Language: Amharic

Book: Genesis


Genesis

Chapter 1

1 እግዚአብሔር በመጀመሪያ ሰማይንና ምድርን ፈጠረ። 2 ምድርም ቅርፅ የሌላትና ባዶ ነበረች። ጥልቅ የሆነው ስፍራዋም በጨለማ ተውጦ ነበር። የእግዚአብሔርም መንፈስ በውሃው ላይ ሰፍፎ ነበር። 3 እግዚአብሔርም፦ “ብርሃን ይሁን” አለ፤ ብርሃንም ሆነ። 4 እግዚአብሔርም ብርሃኑ መልካም እንደሆነ አየ፤ ብርሃንኑም ከጨለማ ለየው። 5 እግዚአብሔርም ብርሃኑን ‘ቀን’ ጨለማውን ደግሞ ‘ሌሊት’ ብሎ ጠራው። ቀኑ መሸ ሌሊቱም ነጋ አንድ ቀን ሆነ። 6 እግዚአብሔርም፦ “በውሆች መካከል ጠፈር ይሁን፣ ውሆችንም ይለያዩ” አለ። 7 እግዚአብሔር ጠፈርን አደረገና ከጠፈር በላይና ከጠፈር በታች ያሉትን ውሆች ለየ። እንደዚያም ሆነ። 8 እግዚአብሔር ጠፈሩን ‘ሰማይ’ብሎ ጠራው። ቀኑ መሸ ሌሊቱም ነጋ ሁለተኛ ቀን። 9 እግዚአብሔር፦ “ከሰማይ በታች ያለው ውሃ ወደ አንድ ስፍራ ይሰብሰብ፣ ምድሩም ይገለጥ” አለ። እንደዚያም ሆነ። 10 እግዚአብሔርም ምድሩን ‘የብስ’፣ ወደአንድ ስፍራ የተሰበሰበውንም ውሃ ‘ባሕር’ ብሎ ጠራው። ይህም መልካም መሆኑን ተመለከተ። 11 እግዚአብሔር፦ እንደ ዓይነታቸው ዘርን የሚያፈሩ ተክሎችን፣ በውስጣቸው ዘርን ያዘሉ የፍራፍሬ ዛፎችን እንደዓይነታቸው የሚያፈሩ አዝርዕትን ታብቅል” አለ። እንደዚያም ሆነ። 12 ምድር እንደአይነታቸው የሚያፈሩ አዝርዕትን አበቀለች። ይህም መልካም እንደሆነ እግዚአብሔር ተመለከተ። 13 ቀኑ መሸ፣ ሌሊቱም ነጋ ሶስተኛ ቀን ሆነ። 14 እግዚአብሔር፦ “ቀኑን ከሌሊቱ ይለዩ ዘንድ በሰማይ ብርሃናት ይሁኑ። እነዚህ ብርሃናት የዓመት ወቅቶችን፣ ቀናትንና ዓመታትን የሚለዩ ምልክቶች ይሁኑ። 15 ለምድርም ብርሃን ይሰጡ ዘንድ በሰማይ ላይ የሚገኙ ብርሃናት ይሁኑ” አለ። እንደዚያም ሆነ። 16 እግዚአብሔር ታላቁ ብርሃን በቀን፣ ታናሹ ብርሃን በሌሊት ይሠለጥኑ ዘንድ ሁለት ታላላቅ ብርሃናትን አደረገ። ከዋክብትንም ደግሞ አደረገ። 17 ለምድርም ብርሃን ይሰጡ ዘንድና 18 በቀንና በሌሊት ላይ እንዲሠለጥኑ እንደዚሁም ብርሃንን ከጨለማ እንዲለዩ በሰማይ አኖራቸው። እግዚአብሔር ይህ መልካም እንደሆነ ተመለከተ። 19 ቀኑ መሸ፣ ሌሊቱም ነጋ አራተኛ ቀን ሆነ። 20 እግዚአብሔር፦ “ውሆች በሕያዋን ፍጡራን የተሞሉ ይሁኑ፣ ወፎችም ከምድር በላይ ባለው በሰማይ ጠፈር ይብረሩ” አለ። 21 እግዚአብሔር ታላላቅ የባሕር ፍጥረታትን እንደዚሁም በምድር የሚንቀሳቀሱ፣ በውሆች ውስጥ የሚርመሰመሱና በክንፎቻቸው የሚበሩ ወፎችን እንደዓይነታቸው ፈጠረ። እግዚአብሔር ይህ መልካም እንደሆነ ተመለከተ። 22 እግዚአብሔርም፦ “ብዙ ተባዙ የባሕርን ውሆች ሙሉአቸው፣ ወፎችም በምድር ላይ ይብዙ” ብሎ ባረካቸው። 23 ቀኑ መሸ፣ ሌሊቱም ነጋ አምስተኛ ቀን ሆነ። 24 እግዚአብሔርም፦ “ምድር እንደወገናቸው ሕያው ፍጥረታትን ማለትም ከብቶችን፣ በምድር ላይ የሚሳቡትንና የምድር አራዊትን ታስገኝ” አለ። እንደዚያም ሆነ። 25 እግዚአብሔር በየዓይነታቸው የምድር አራዊትን፣ በየዓይነታቸው ማናቸውንም በምድር የሚሳቡትን ፈጠረ። 26 እግዚአብሔርም፦ “ሰውን በመልካችን እንደ አምሳላችን እንፍጠር፣ ሰዎችም በባሕር ዓሣዎች፣ በሰማይ በሚበሩ ወፎችና በምድር ላይ በሚሳቡ ማናቸውም ተሳቢ ፍጥረቶች ላይ ሥልጣን ይኑራቸው” አለ። 27 እግዚአብሔር ሰውን በራሱ መልክ፣ በራሱም አምሳል ፈጠረው። ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው። 28 እግዚአብሔር ባረካቸው እንደዚህም አላቸው፦ “ብዙ ተባዙ፣ ምድርንም ሙሉአት ግዟትም። በባሕር ውስጥ ባሉት ዓሣዎች፣ በሰማይ ላይ በሚበሩት ወፎችና በምድር ላይ በሚንቀሳቀሱት ማናቸውም ሕያዋን ፍጥረቶች ሁሉ ላይ ሥልጣን ይኑራችሁ” 29 እግዚአብሔርም፦ “እነሆ፣ ምግብ ይሆኑላችሁ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ በውስጣቸው ዘርን ያዘሉ ማናቸውንም ተክሎችና በውስጣቸው ፍሬ ያላቸውን ማናቸውንም የፍራፍሬ ዛፎች ሰጥቻችኋለሁ። 30 በምድር ላይ ለሚገኙ እንስሳት ሁሉ፣ በሰማይ ለሚበሩ ወፎች ሁሉ፣ እንዲሁም በምድር ላይ ለሚሳቡ ፍጥረታት ሁሉ ማለትም የሕይወት እስትንፋስ ላለበት ማንኛውም ፍጡር ማንኛውም ለምለም ተክል ምግብ እንዲሆናቸው ሰጥቻለሁ። እንደዚሁም ሆነ። 31 እግዚአብሔር የፈጠረውን ማንኛውንም ነገር ተመለከተ። እነሆ፣ እጅግ መልካም ነበረ። ቀኑ መሸ፣ ሌሊቱም ነጋ ስድስተኛ ቀን ሆነ።



Chapter 2

1 የምድር በውስጣቸው ያሉትም ሕያዋን ፍጡራን አፈጣጠር በዚህ ሁኔታ ተከናወነ። 2 እግዚአብሔር ይሠራ የነበረውን ሥራ በሰባተኛው ቀን ፈጽሞ በዚሁ ቀን ከሥራው ሁሉ አረፈ። 3 እግዚአብሔር የመፍጠር ሥራውን ሁሉ ፈጽሞ ያረፈው በዚህ ቀን ስለሆነ ሰባተኛውን ቀን ባረከው ቀደሰውም። 4 እግዚአብሔር አምላክ ሰማይንና ምድርን በፈጠረበት ወቅት የሰማይና የምድር የአፈጣጠራቸው ታሪክ እንደዚህ ነበር። 5 እግዚአብሔር አምላክ በምድር ላይ ዝናብ እንዲዘንብ ስላደረገና ምድርንም የሚያለማ ሰው ባለመኖሩ በምድር ላይ ምንም ቡቃያ አልነበረም፣ በምድር ላይ የሚበቅል ተክልም ገና አልበቀለም። 6 ነገር ግን ውሃ ከመሬት እየመነጨ የምድርን ገጽ ያረሰርስ ነበር። 7 እግዚአብሔር አምላክም ከምድር አፈር ሰውን አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስ እፍ አለበት፤ ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ። 8 እግዚአብሔር አምላክም በስተምሥራቅ በኩል በዔደን የአትክልት ስፍራ አዘጋጀ፣ የአበጀውንም ሰው በዚያ አኖረው። 9 ከምድር ውስጥም እግዚአብሔር አምላክ ለዓይን የሚያስደስቱና ለምግብነት የሚጠቅሙ ልዩ ልዩ ዛፎች እንዲበቅሉ አደረገ። በአትክልት ስፍራው መካከልም የሕይወት ዛፍ ነበር፣ መልካሙንና ክፉውን የሚያሳውቀውም ዛፍ በዚያ ነበር። 10 የአትክልት ስፍራውንም የሚያጠጣ ወንዝ ከኤደን ይፈስ ነበር። ወንዙም ከኤደን ከወጣ በኋላ አራት ወንዞች ሆኖ ይከፋፈል ነበር። 11 የመጀመሪያው ፊሶን የተባለው ወንዝ ነበር፣ ይህም ወርቅ ይገኝበት የነበረውን መላውን የሐዊላ ምድር አቋርጦ የሚፈስው ወንዝ ነበር። 12 የዚያ አገር ወርቅ የጠራ ወርቅ ነበር፤ በተጨማሪም በዚያ አገር ሽቶና የከበሩ ድንጋዮች ነበሩ። 13 የሁለተኛው ወንዝ ስም ግዮን ይባል ነበር፣ እርሱም መላውን የኢትዮጵያ ምድር አቋርጦ ይፈስ ነበር። 14 የሶስተኛው ወንዝ ስም ጤግሮስ ይባል ነበር፣ እርሱም በአሦር በስተምሥራቅ ይፈሳል። አራተኛው ወንዝ ኤፍራጥስ ነበር። 15 እግዚአብሔር አምላክም የኤደንን የአትክልት ስፍራ ያለማና ይንከባከብ ዘንድ ሰውን ወስዶ በዚያ አኖረው። 16 እግዚአብሔር አምላክም እንዲህ በማለት አዘዘው፣ “በአትክልቱ ስፍራ ካለው ከማንኛውም የፍሬ ዛፍ መብላት ትችላልህ። 17 ነገር ግን መልካሙንና ክፉውን ከሚያሳውቀው ዛፍ አትብላ፣ ምክንያቱም ከእርሱ በበላህ ቀን በእርግጥ ትሞታለህ።” 18 ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ፦ “ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም። ስለዚህ የምትመቸውን ረዳት እፈጥርለታለሁ” አለ። 19 እግዚአብሔር አምላክም ከምድር አፈር የምድር እንስሶችንና የሰማይ ወፎችን አበጀ። ምን ስም እንደሚያወጣላቸው ይመለከት ዘንድ ወደ አዳም አመጣቸው። ለእያንዳንዱ ሕያው ፍጡር አዳም ያወጣለት ስም ያ ስሙ ሆነ። 20 አዳም ለሁሉም ከብቶች፣ ለሁሉም የሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት ሁሉ ስም አወጣላቸው። ነገር ግን ለአዳም ለራሱ የምትመች ረዳት አልተገኘለትም። 21 እግዚአብሔር አምላክ በአዳም ላይ ከባድ እንቅልፍ እንዲወስደው አደረገ፣ ስለሆነም አዳም አንቀላፋ። እግዚአብሔር አምላክ አዳም አንቀላፍቶ ሳለ ከጎድን አጥንቶቹ አንዱን ወስዶ አጥንቱን የወሰደበትን ስፍራ በሥጋ ዘጋው። 22 እግዚአብሔር አምላክ ከአዳም ከወሰደው የጎድን አጥንት ሴት አድርጎ ሠራት። ወደ አዳምም አመጣት። 23 አዳምም፦ “አሁን ይህቺ ከአጥንቴ የተገኘች አጥንት ከሥጋዬ የተገኘች ሥጋ ናት። ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል” አለ። 24 ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይጣመራል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ። 25 አዳምና ሚስቱ ሁለቱም ራቁታቸውን ነበሩ፤ ይሁን እንጂ አይተፋፈሩም ነበር።



Chapter 3

1 እግዚአብሔር በምድር ላይ ከፈጠራቸው ማናቸውም ሌሎች አራዊቶች ሁሉ ይልቅ እባብ ተንኮለኛ ነበር። እርሱም ሴቲቱን፦ “በእርግጥ እግዚአብሔር ‘በአትክልቱ ስፍራ ካለው ከማንኛውም ዛፍ አትብሉ’ ብሎአልን?” ብሎ ጠየቃት። 2 ሴቲቱም ለእባቡ፦ “በአትክልቱ ስፍራ ካሉት የዛፎች ፍሬዎች መብላት እንችላለን፤ 3 ነገር ግን በአትክልቱ ስፍራ መካከል ስለሚገኘው ዛፍ እግዚአብሔር “እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ አትንኩትም” ብሎአል። 4 እባብም ለሴቲቱ፦ “በፍጹም አትሞቱም። 5 ከእርሱ በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንደሚከፈቱ እንደ እግዚአብሔርም መልካሙንና ክፉውን የምታውቁ እንደምትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው አላት።” 6 ሴቲቱም ዛፉ ለመብላት መልካም፣ ሲያዩት ደስ የሚያሰኝና ጥበብንም ለማግኘት የሚያጓጓ እንደሆነ ተመልክታ ከፍሬው ወስዳ በላች፤ ከእርሷ ጋር ለነበረውም ለባሏ ከፍሬው ሰጠችው፣ እርሱም በላ። 7 የሁለቱም ዓይኖች ተከፈቱ፣ ራቁታቸውን እንደነበሩም አወቁ። የበለስ ቅጠሎችንም በማጋጠም ከሰፉ በኋላ ለራሳቸው መሸፈኛ ግልድም ሠሩ። 8 ቀኑ ወደ ምሽት ሲቃረብ በአትክልት ስፍራው ሲመላለስ የእግዚአብሔር አምላክን ድምፅ ሰሙ፤ ስለዚህ አዳምና ሚስቱ ከእግዚአብሔር አምላክ ፊት በመሸሽ በአትክልቱ ስፍራ በነበሩት ዛፎች መካከል ተሸሸጉ። 9 እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ጠራውና፣ “የት ነህ?” አለው። 10 አዳምም፣ “በአትክልቱ ስፍራ ውስጥ ድምፅህን ሰማሁና ራቁቴን ስለነበርሁ ፈራሁ፤ በዚህም ምክንያት ተሸሸግሁ።” 11 እግዚአብሔርም፦ “ራቁትህን እንደሆንክ ማን ነገረህ? ከእርሱ እንዳትበላ ብዬ ካዘዝኩህ ከዛፉ ፍሬ በላህን?” አለው። 12 አዳምም፦ “አብራኝ እንድትሆን የሰጠኸኝ ሴት ከዛፉ ፍሬ ሰጠችኝ፣ እኔም በላሁት” አለ። 13 እግዚአብሔር አምላክም ሴቲቱን፦ “ምንድነው ያደረግሽው?” አላት። ሴቲቱም፦ “እባቡ አታለለኝና በላሁ” አለች። 14 እግዚአብሔር አምላክም ለእባቡ፦ “ይህንን በማድረግህ ከእንስሳት ሁሉና ከምድር አራዊት ሁሉ ተለይተህ የተረገምህ ትሆናለህ። በደረትህ እየተሳብክ ትሄዳለህ፣ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ አፈር ትበላለህ። 15 በአንተና በሴቲቱ፣ በዘርህና በዘሯ መካካል ጠላትነትን አደርጋለሁ። የእርሷ ዘር ራስህን ይቀጠቅጣል፣ አንተም ተረከዙን ትነክሳለህ” አለው። 16 ለሴቲቱም እንዲህ አላት፦ “በምጥ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛለሁ፤ በስቃይም ትወልጃለሽ። ፈቃድሽ ወደ ባልሽ ይሆናል፣ እርሱም ገዢሽ ይሆናል።” 17 ለአዳምም እንደዚህ አለው፦ “የሚስትህን ቃል ሰምተህ ‘ከእርሱ እንዳትበላ’ ብዬ ካዘዝሁህ ከዛፉ ፍሬ ስለበላህ ከአንተ የተነሳ ምድር የተረገመች ትሁን፤ በሕይወትህ ዘመን ሁሉ በከባድ ድካም ምግብህን ከእርሷ ታገኛለህ። 18 ምድር እሾህና አሜኬላ ታበቅልብሃለች፤ የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ። 19 ከተገኘህበት አፈር እስክትመለስ ድረስ በላብህ እንጀራን ትበላለህ። አፈር ነህና ወደ አፈር ተመልሰህ ትሄዳለህ”። 20 የሕያዋን ሁሉ እናት በመሆኗ አዳም ለሚስቱ ‘ሔዋን’ የሚል ስም አወጣላት። 21 እግዚአብሔር አምላክ ከቆዳ ልብስ አዘጋጅቶ አዳምንና ሚስቱን አለበሳቸው። 22 እግዚአብሔር አምላክ፦ “መልካምንና ክፉውን ለይቶ በማውቅ ረገድ አሁን ሰው ከእኛ እንደ አንዱ ሆኖአል። ስለዚህ አሁን እጁን ዘርግቶ ከሕይወት ዛፍ ፍሬ ቀጥፎ እንዳይበላ ለዘላለምም እንዳይኖር ሊፈቀድለት አይገባም” አለ። 23 በዚህም ምክንያት የተገኘባትን ምድር እንዲያለማ እግዚአብሔር አዳምን ከኤደን የአትክልት ስፍራ አስወጣው። 24 ስለዚህ እግዚአብሔር አዳምን ከአትክልት ስፍራው አባረረው፣ ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደውንም መንገድ ይጠብቁ ዘንድ ከኤደን የአትክልት ስፍራ በስተቀኝ በኩል ኪሩቤልን እንደዚሁም በየአቅጣጫው የምትገለባበጥ ነበልባላዊ ሰይፍ አኖረ።



Chapter 4

1 አዳምም ከሚስቱ ከሔዋን ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጸመ። እርሷም ፀነሰች። ቃየንንም ወለደች። “በእግዚአብሔር ዕርዳታ ወንድ ልጅ ወለድሁ” አለች። 2 ከዚያ በኋላም ወንድሙን አቤልን ወለደች። አቤል የበግ እረኛ ሲሆን ቃየን ግን ገበሬ ሆነ። 3 ከዕለታት አንድ ቀን ቃየን ከምድር ፍሬ ለእግዚአብሔር መባ አቀረበ። 4 አቤል ደግሞ መጀመሪያ ከተወለዱ በጎች መካከል ስባቸውን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ። እግዚአብሔር በአቤልና በመሥዋዕቱ ደስ ተሰኘ፣ 5 በቃየንና በመሥዋዕቱ ግን ደስ አልተሰኘም። ስለዚህ ቃየን በጣም ተቆጣ፣ ፊቱም ተኮሳተረ። 6 እግዚአብሔር አምላክ ቃየንን፦ “ለምን ተቆጣህ፣ ፊትህስ ለምን ተኮሳተረ? 7 መልካም ብታደርግ ፊትህ ያበራ አልነበረምን? ያደረግኸው መልካም ካልሆን ግን ኃጢአት በደጅህ እያደባች ናት፣ ልትቆጣጠርህም ትፈልጋለች፣ አንተ ግን በቁጥጥርህ ሥር አድርጋት” አለው። 8 ቃየን ወንድሙን አቤልን፦ “ወደ ሜዳ እንውጣ” አለው፣ በዚያም ቃየን በወንድሙ በአቤል ላይ በቁጣ ተነሳበት፣ ገደለውም። 9 ከዚያ በኋላም እግዚአብሔር ቃየንን፦ “ወንድምህ አቤል ወዴት ነው?” አለው። እርሱም፦ “አላውቅም፣ እኔ የወንድሜ ጠባቂ ነኝን?” አለ። 10 እግዚአብሔርም፦ “ያደረግኸው ምንድን ነው? የወንድምህ ደም ከምድር ወደ እኔ ይጮኻል” አለው። 11 “አሁንም የወንድምህን ደም ከእጅህ ለመቀበል አፍዋን በከፈተች በምድር ላይ አንተ የተረገምህ ነህ። 12 ምድርንም በምታርስበት ጊዜ ፍሬዋን በሙላት አትሰጥህም። በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች ትሆናለህ” አለው። 13 ቃየንም ለእግዚአብሔር፦ ቅጣቴ ከምችለው በላይ ነው። 14 በእርግጥም ዛሬ ከምድሪቱ አባርረኸኛል፣ እኔም ከፊትህ እሸሸጋለሁ። በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች እሆናለሁ፣ የሚያገኘኝም ሁሉ ይገድለኛል” አለው። 15 እግዚአብሔርም፦ “ቃየንን የሚገድል ማንኛውም ሰው ሰባት እጥፍ የበቀል እርምጃ ይወሰድበታል” አለ። ከዚያ በኋላም የሚያገኘው ማንኛውም ሰው እንዳይገድለው እግዚአብሔር በቃየን ላይ ምልክት አደረገበት። 16 ቃየንም ከእግዚአብሔር ፊት ወጥቶ ሄደ፣ ከኤደን በስተምሥራቅ በነበረው ኖድ በተባለው ምድር ኖረ። 17 ቃየንም ከሚስቱ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጸመ፣ እርሷም ፀነሰች፣ ሄኖክንም ወለደች። ቃየን ከተማን መሠረተ፣ የመሠረታትንም ከተማ በልጁ ስም ሄኖክ ብሎ ጠራት። 18 ሄኖክም አራድን ወለደ። አራድም መሑያኤልን ወለደ። መሑያኤልም መቱሳኤልን ወለደ። መቱሳኤልም ላሜክን ወለደ። 19 ላሜክም ዓዳና ጺላ የተባሉ ሁለት ሚስቶችን አገባ። 20 ዓዳ ያባልን ወለደች፣ እርሱም በድንኳን ለሚኖሩ ለከብት አርቢዎች አባት ነበር። 21 የእርሱ ወንድም ዩባልም የበገና ደርዳሪዎችና የዋሽንት ነፊዎች አባት ነበር። 22 ጺላም ከነሐስና ከብረት መሣሪያዎችን የሚሠራውን ቱባልቃይንን ወለደች። የቱባልቃይንም እህት ናዕማ ትባል ነበር። 23 ላሜክ ለሚስቶቹ፦ “አዳና ጺላ ስሙኝ፣ እናንተ የላሜክ ሚስቶች የምላችሁን ስሙኝ ስለጎዳኝና ስላቆሰለኝ አንድ ሰው ገድያለሁ። 24 ቃየንን የሚገድል ሰባት እጥፍ የበቀል እርምጃ የሚወሰድበት ከሆነ የላሜክ ገዳይማ ሰባ ሰባት እጥፍ የበቀል እርምጃ ይወሰድበታል” አላቸው። 25 አዳም ከሚስቱ ጋር እንደገና የግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጸመ፣ እርሷም ወንድ ልጅ ወለደች። “ቃየን በገደለው በአቤል ፈንታ እግዚአብሔር ምትክ ሰጠኝ” በማለት ስሙን ሤት ብላ ጠራችው። 26 ለሤትም ወንድ ልጅ ተወለደለት፣ ስሙንም ሄኖስ አለው። በዚያም ዘመን ሰዎች የእግዚአብሔርን ስም መጥራት ጀመሩ።



Chapter 5

1 የአዳም የትውልድ ሐረግ እንደሚከተለው ነው። እግዚአብሔር ሰውን በፈጠረው ጊዜ በራሱ አምሳያ ፈጠራቸው፤ 2 ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው፣ ባረካቸውም። በተፈጠሩም ጊዜ ‘ሰው’ ብሎ ጠራቸው። 3 አዳም ዕድሜው 130 ዓመት በሆነ ጊዜ፣ እርሱን የሚመስል ወንድ ልጅ ወለደ፣ ስሙንም ‘ሤት’ ብሎ ጠራው። 4 አዳም ሤትን ከወለደ በኋላ 800 ዓመታት ኖረ። ሌሎችን ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ፤ 5 930 ዓመት ሲሆነውም ሞተ። 6 ሤት ዕድሜው 105 ሲሆን ሄኖስን ወለደ። 7 ሄኖስን ከወለደ በኋላ ሤት 807 ዓመት ኖረ። ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 8 ሤት 912 ዓመታት ከኖረ በኋላ ሞተ። 9 ሄኖስ 90 ዓመት ሲሆነው ቃይናንን ወለደ። 10 ሄኖስ ቃይናንን ከወለደ በኋላ 815 ዓመታት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 11 ሄኖስ 905 ዓመታት ከኖረ በኋላ ሞተ። 12 ቃይናን 70 ዓመት ሲሆነው መላልኤልን ወለደ። 13 ቃይናን መላልኤልን ከወለደ በኋላ 840 ዓመታት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 14 ቃይናን 910 ዓመታት ከኖረ በኋላ ሞተ። 15 መላልኤል 65 ዓመት ሲሆነው ያሬድን ወለደ። 16 መላልኤል ያሬድን ከወለደ በኋላ 800 ዓመታት ኖረ። ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 17 መላልኤል 895 ዓመታት ከኖረ በኋላ ሞተ። 18 ያሬድ 162 ዓመት ሲሆነው ሄሮክን ወለደ። 19 ያሬድ ሄኖክን ከወለደ በኋላ 800 ዓመታት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 20 ያሬድ 962 ዓመታት ከኖረ በኋላ ሞተ። 21 ሄኖክ 65 ዓመት ሲሆነው ማቱሳላን ወለደ። 22 ሄኖክ ማቱሳላን ከወለደ በኋላ የእግዚአብሔርን መንገድ በመከተል 300 ዓመታት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 23 ሄኖክ 365 ዓመታት ኖረ። 24 ሄኖክ የእግዚአብሔርን መንገድ በመከተል ኖረ፣ ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ስለወሰደው አልተገኘም። 25 ማቱሳላ 187 ዓመት ሲሆነው ላሜሕን ወለደ። 26 ማቱሳላ ላሜሕን ከወለደ በኋላ 782 ዓመታት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 27 ማቱሳላ 969 ዓመታት ከኖረ በኋላ ሞተ። 28 ላሜሕ 182 ዓመት ሲሆነው አንድ ወንድ ልጅ ወለደ። 29 “ይህ ልጅ እግዚአብሔር በረገማት ምድር ከልፋታችንና ከብርቱ ሥራችን ያሳርፈናል” ሲል ስሙን ‘ኖህ’ ብሎ ጠራው። 30 ላሜሕ ኖህን ከወለደ በኋላ 595 ዓመታት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 31 ላሜሕ 777 ዓመታት ከኖረ በኋላ ሞተ። 32 ኖህ 500 ዓመታት ሲሆነው ሴም፣ ካምንና ያፌትን ወለደ።



Chapter 6

1 የሰው ልጆች በምድር ላይ እየበዙ ሲሄዱ ሴቶች ልጆች ተወለዱላቸው። 2 የእግዚአብሔር ልጆችም የሰዎች ሴቶች ልጆች የሚስብ ውበት እንዳላቸው ተመለከቱ። ከእነርሱ መካከልም የመረጧቸውን ሚስቶች አድርገው ወሰዱ። 3 እግዚአብሔርም፦ “እርሱ ሥጋ ስለሆነ መንፈሴ በሰው ላይ ለዘላለም አይኖርም፤ ዕድሜውም 120 ዓመት ይሆናል” አለ። 4 የእግዚአብሔር ልጆች ከሰዎች ሴቶች ልጆች ጋብቻ በፈጸሙና ልጆችን በወለዱበት በዚያን ጊዜ ከዚያም በኋላ ኔፊሊም የተባሉ ግዙፍ ሰዎች በምድር ላይ ነበሩ። እነርሱም በጥንት ዘመን ዝናን ያተረፉ ኅያላን ነበሩ። 5 እግዚአብሔር የሰው ልጆች ክፋት በምድር ላይ እየበዛ እንደሆነና የልቡም ሃሳብ ዘወትር ወደ ክፋት ብቻ ያዘነበለ መሆኑን ተመለከተ። 6 እግዚአብሔር የሰው ልጆችን በምድር ላይ በመፍጠሩ ተጸጸተ ልቡም አዘነ። 7 በዚህም ምክንያት እግዚአብሔር፦ “የፈጠርሁትን የሰው ልጅ ከምድር ገጽ አጠፋለሁ፤ ስለፈጠርኋቸው ተጸጽቻለሁና ከእነርሱም ጋር እንስሳትን፣ በደረታቸው የሚሳቡትን ፍጥረታትና የሰማይ ወፎችን ሁሉ አጠፋለሁ” አለ። 8 ኖኅ ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስ አገኘ። 9 የኖኅ ታሪክ እንደሚከተለው ነው። ኖኅ በዘመኑ ከነበሩት ሰዎች ሁሉ ይልቅ ጻድቅና ከበደል የራቀ ሰው ነበር፤ የእግዚአብሔርንም መንገድ የሚከተል ሰው ነበር። 10 ኖኅ ሴም፣ ካምና ያፌት የተባሉትን ሶስት ወንዶች ልጆች ወለደ። 11 በእግዚአብሔር ፊት በክፉ ሥራ ረከሰች በዓመፅም ተሞላች። 12 እግዚአብሔር ምድርን ተመለከተ፣ የተበላሸች እንደሆነችና በምድር የሚኖሩትም ሰዎች ሁሉ በክፋት እንደሚኖሩ አየ። 13 እግዚአብሔርም ኖኅን፦ “ሥጋን የለበሰ ሁሉ ፍጻሜ ደርሶአል፣ ከእነርሱ የተነሳ ምድር በግፍ ተሞልታለችና። እኔም በእርግጥ ከምድር ጋር አጠፋቸዋለሁ። 14 አንተ ግን ከጥሩ እንጨት መርከብ ሥራ፤ መርከቧም ክፍሎች እንዲኖራት አድርግ፤ ውስጧንና ውጭዋንም በቅጥራን ለቅልቀው። 15 እንደዚህ አድርገህ ሥራት፦ ርዝመቷ 140 ሜትር፣ ወርዷ 23 ሜትር፣ ከፍታዋ 13. 5 ሜትር ይሁን። 16 ለመርከቧ ጣራ አብጅላት፣ ጣራና ግድግዳው በሚጋጠምበት ቦታ ግማሽ ሜትር ክፍተት ተው፤ ከጎኗ በር አውጣላት፤ ባለ ሦስት ፎቅ አድርገህ ሥራት። 17 እኔም ከሰማይ በታች የሕይወት እስትንፋስ ያለባችውን ፍጡራን ሁሉ ለማጥፋት እነሆ በምድር ላይ የጥፋት ውሃ አወርዳለሁ፤ በምድር ላይ ያለ ሁሉ ይጠፋል። 18 ከአንተ ጋር ግን ቃል ኪዳን እገባለሁ፤ አንተና ሚስትህ፣ ልጆችህና የልጆችህ ሚስቶች ከአንተ ጋር ወደ መርከቧ ትገባላችሁ። 19 ከአንተ ጋር በሕይወት እንዲቆዩ ከሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ወንድና ሴት እያደረግህ ሁለት ሁለቱን ወደ መርከቧ ታስገባለህ። 20 ከእያንዳንዱ የወፍ ወገን፣ ከእያንዳንዱ የእንስሳ ወገን፣ በምድር ላይ ከሚሳቡ ፍጥረት ሁሉ በየወገናቸው በሕይወት ይቆዩ ዘንድ ወደ አንተ ይምጡ። 21 ለአንተና ለእነዚህ ፍጥረቶች ሁሉ የሚበቃ ልዩ ልዩ ዓይነት ምግብ በመርከቡ ውስጥ አከማች።” 22 ኖኅም እግዚአብሔር ያዘዘውን ሁሉ አደረገ።



Chapter 7

1 እግዚአብሔር ኖኅን እንዲህ አለው፦ “በዚህ ትውልድ መካከል አንተን ጻድቅ ሆነህ አግኝቼሃለሁና ቤተሰብህን በሙሉ ይዘህ ወደ መርከቧ ግባ። 2 ከንፁህ እንስሳት ሁሉ ሰባት ሰባት ወንድና ሴት፣ ንፁሕ ካልሆኑት እንስሳት ደግሞ ሁለት ሁለት ወንድና ሴት ከአንተ ጋር አስገባ። 3 እንዲሁም ከሰማይ ወፎች ወገን ሰባት ወንዶችና ሰባት ሴቶች በምድር ላይ ለዘር እንዲተርፉ ከአንተ ጋር ታስገባለህ። 4 ከሰባት ቀን በኋላ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በመድር ላይ ዝናብ አዘንባለሁ፤ የፈጠርሁትንም ሕያው ፍጡር ሁሉ ከምድር ላይ አጠፋለሁ።” 5 ኖኅም እግዚአብሔር ያዘዘውን ሁሉ አደረገ። 6 የጥፋት ውሃ በምድር ላይ በወረደ ጊዜ ኖኅ የ600 ዓመት ሰው ነበር። 7 ኖኅና ወንዶች ልጆቹ ሚስቱና የልጆቹ ሚስቶች ከጥፋት ውሃ ለማምለጥ ወደ መርከቡ ገቡ። 8 ንፁሕ ከሆኑትና ንፁሕ ካልሆኑት እንስሳት ከወፎችና በምድር ላይ ከሚሳቡ ፍጡራን ሁሉ 9 ጥንድ ጥንድ ወንድና ሴት ሆነው ወደ ኖኅ መጡ፤ እግዚአብሄር ኖኅን ባዘዘው መሠረትም ወደ መርከቧ ገቡ። 10 ከሰባት ቀንም በኋላ የጠፋት ውሃ በምድር ላይ መጣ። 11 ኖኅ በተወለደ በ600ኛው ዓመት በሁለተኛው ወር ከወሩም በአሥራ ሰባተኛው ቀን የታላቁ ጥልቅ ምንጮች በሙሉ ተነደሉ፤ የሰማይ መስኮቶችም ተከፈቱ። 12 ዝናቡም መዝነብ ጀመረ፣ አርባ ቀንና አርባ ሌሊትም ባለማቋረጥ በምድር ላይ ዘነበ። 13 ዝናቡ መዝነብ በጀመረበት ቀን ኖኅና ሚስቱ ከልጆቻቸው ጋር ከሴም ከካም ከያፌትና ከሶስቱም ልጆቻቸው ሚስቶች ጋር ወደ መርከቡ ገቡ። 14 ከአራዊት ከእንስሳት በደረታቸው እየተሳቡ ከሚንቀሳቀሱ ፍጥረቶችና በሰማይ ከሚበሩ ወፎች ከእያንዳንዱ ዓይነት አብረዋቸው ገቡ። 15 የሕይወት እስትንፋስ ያለባቸው ፍጡራን በሙሉ ጥንድ ጥንድ እየሆኑ ከኖኅ ጋር ወደ መርከቡ ገቡ። 16 ከሕያዋንም ፍጡራን ሁሉ እግዚአብሔር ኖኅን ባዘዘው መሠረት ወንድና ሴት እየሆኑ ገቡ፤ ከዚያም እግዚአብሔር የመርከቡን በር ከውጭ ዘጋ። 17 የጥፋት ውሃም ለአርባ ቀናት ያለመቋረጥ በምድር ላይ ዘነበ ውሃው እየጨመረ በሄድ መጠን መርከቧን ከምድር ወደ ላይ አነሳት። 18 ውሃው በምድር ላይ በጣም እየጨመረና ከፍ እያለ ሲሄድ፣ መርከቧ በውሃ ላይ ተንሳፈፈች። 19 ውሃው በጣም ከፍ በማለቱ፣ ከሰማይ በታች ያሉትን ታላላቅ ተራሮች ሁሉ ሸፈናቸው። 20 ውሃው ከተራሮች ጫፍ በላይ 7ሜትር ያህል ከፍ አለ። 21 በምድር ላይ የነበሩ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ፦ ወፎች፣ የቤት እንስሳት፣ አራዊት፣ በምድር የሚርመሰመሱ ፍጡራን ሰዎችም በሙሉ ጠፉ። 22 የሕይወት እስትንፋስ ያላቸው በምድር የነበሩ ፍጡራን ሁሉ ሞቱ። 23 ሕይወት ያላቸው ፍጡራን ሁሉ ከሰዎች ጀምሮ እንስሳት፣ በምድር ላይ የሚሳቡ ፍጡራንና የሰማይ ወፎች ሁሉም ከምድር ገጽ ጠፉ። ኖኅና ከእርሱ ጋር በመርከቧ ውስጥ የነበሩት ብቻ ተረፉ። 24 ውሃውም ምድርን ሸፍኖ መቶ አምሳ ቀን ቆየ።



Chapter 8

1 እግዚአብሔር ኖኅንና ከእርሱ ጋር በመርከቧ ውስጥ የነበሩትን አራዊትና እንስሳት ሁሉ አሰበ። በምድር ላይ ነፋስ እንዲነፍስ አደረገ ውሃውም ጎደለ። 2 የጥልቁ ምንጮችና የሰማይ መስኮቶች ተዘጉ፣ ዝናቡም መዝነቡን አቆመ። 3 ውሃው ከምድር ላይ ቀስ በቀስ እየቀነሰ መጣ፤ ከመቶ ሃምሳ ቀን በኋላም የውሃው ከፍታ እጅግ ቀነሰ። 4 በሰባተኛው ወር፤ በአሥራ ሰባተኛው ቀን መርከቧ በአራራት ተራሮች ላይ አረፈች። 5 ውሃው እስከ አሥረኛው ወር ድረስ ቀስ በቀስ እየጎደለ ሄደ። በአሥረኛው ወር መጀመሪያው ቀን የተራሮች ጫፎች ታዩ። 6 ከአርባ ቀን በኋላ ኖኅ የሠራውን የመርከቧን መስኮት ከፍቶ፣ 7 ቁራን ወደ ውጭ ላከ፤ ቁራውም ውሃው ከምድር ላይ እስኪደርቅ ድረስ ወዲያና ወዲህ ይበር ነበር። 8 ከዚያም በኋላ ኖኅ ውሃው ከምድር ላይ ገጽ ጎድሎ እንደሆነ ለማወቅ ርግብን ላከ፤ 9 ነገር ግን ውሃው ገና ምድርን ሁሉ ሸፍኖ ስለነበር ርግቢቱ የምታርፍበት ቦታ አላገኘችም፤ ስለዚህ ኖኅ ወዳለበት መርከብ ተመልሳ መጣች፤ ኖኅም እጁን ዘርግቶ ወደ መርከቡ ውስጥ አስገባት። 10 ሰባት ቀን ከቆየ በኋላ ኖኅ ርግቧን እንደገና ላካት። 11 እርሷም ወደ ማታ ተመለሰች፤ እነሆም የለመለመ የወይራ ቅጠል በአፏ ይዛ ነበር፤ ከዚህም የተነሣ ኖኅ ውሃው ከምድር ላይ መጉደሉን አወቀ። 12 ደግሞም ሰባት ቀን ከቆየ በኋላ ኖኅ ርግቢቱን እንደገና አውጥቶ ላካት፤ በዚህ ጊዜ ግን ርግቢቱ ወደ እርሱ አልተመለሰችም። 13 ኖኅ በተወለደ 601ኛው ዓመት፣ በመጀመሪያው ወር፣ ከወሩም በመጀመሪያው ቀን ውሃው ከምድር ላይ ደረቀ። ኖኅ የመርከቡን ክዳን አንሥቶ ዙሪያውን ተመለከተ፣ ምድሪቱም እንደደረቀች አየ። 14 በሁለተኛው ወር፣ በሃያ ሰባተኛው ቀን ምድሪቱ ሙሉ በሙሉ ደረቀች። 15 ከዚያም እግዚአብሔር ኖኅን እንዲህ አለው። 16 “አንተና ሚስትህ፣ ልጆችህና የልጆችህ ሚስቶች ከመርከቧ ውጡ። 17 እንዲዋለዱ፣ እንዲራቡና በምድር ላይ እንዲበዙ ከአንተ ጋር ያሉትን ወፎች፣ እንስሳትና በምድር ላይ የሚሳቡ ሕያዋን ፍጡራንን ሁሉ ይዘሃቸው ውጣ።” 18 ስለዚህ ኖኅ ከልጆቹ፣ ከሚስቱና ከልጆቹ ሚስቶች ጋር ወጣ። 19 እንስሳቱ ሁሉ፣ ወፎችም፣ በምድር የሚሳቡት፣ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱ ሕያዋን ፍጥረታት ሁሉ በየወገናቸው ከመርከቧ ወጡ። 20 ኖኅም ለእግዚአብሔር መሠዊያን ሠራ። ንፁሕ ከሆኑት እንስሳትና ንፁሕ ከሆኑት ወፎች አንዳንዶቹን ወስዶ የሚቃጠል መሥዋዕት አቀረበ። 21 እግዚአብሔርም ደስ የሚያሰኘውን መዓዛ አሸተተ፣ በልቡም እንዲህ አለ፦ “ምንም እንኳ ሰው ገና ከልጅነቱ ጀምሮ ሐሳቡ ወደ ክፋት ያዘነበለ ቢሆንም በእርሱ ምክንያት ሁለተኛ ምድርን አልረግማትም፤ አሁን እንዳደረግሁት ሕያዋን ፍጡራንን ዳግመኛ አላጠፋም። 22 ምድር እስካለች ድረስ የዘር ወቅትና መከር፣ ሙቀትና ቅዝቃዜ፣ በጋና ክረምት፣ ቀንና ሌሊት አይቋረጡም።”



Chapter 9

1 ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር ኖኅንና ልጆቹን እንዲህ ሲል ባረካቸው፦ “ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሏት፤ 2 አስፈሪነታችሁና አስደንጋጭነታችሁ በእንስሳት፣ በሰማይ ወፎች፣ በደረት በሚሳቡ ተንቀሳቃሽ ፍጡሮችና በባሕር ዓሦች፣ በምድር ላይ በሚገኙ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ላይ ይሁን። ሁሉም በሥልጣናችሁ ሥር ይሁኑ። 3 ሕያውና ተንቀሳቃሽ ፍጡር ሁሉ ምግብ ይሁናችሁ፣ ለምለሙን ዕፅዋት እንደሰጠኋችሁ፣ አሁን ደግሞ ሁሉን ሰጠኋችሁ። 4 ነገር ግን ሕይወቱ ማለት ደሙ ገና በውስጡ ያለበትን ሥጋ አትብሉ። 5 ሰውን የገደለ ሁሉ ስለሟቹ ደም ተጠያቂ ነው፤ የሟቹን ሰው ደም ከገዳዩ ከእንስሳም ይሁን ከሰው እሻለሁ። 6 የሰውን ደም የሚያፈስ ሁሉ ደሙ በሰው እጅ ይፈሳል፤ በእግዚአብሔር አምሳል እግዚአብሔር ሰውን ሠርቶታልና። 7 እናንተ ግን ብዙ ተባዙ፣ ዘራችሁ በምድር ላይ ይብዛ ይንሠራፋም።” 8 ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር ለኖኅና ለልጆቹ እንዲህ አላቸው፦ 9 “እነሆ ከእናንተና ከእናንተ በኋላ ከሚመጣው ዘራችሁ ጋር ኪዳኔን እመሠርታለሁ፤ 10 እንዲሁም ከእናንተ ጋር ከነበሩት ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ከወፎች፣ ከእንስሳት ከእናንተ ጋር ከመርከቧ ከወጡት በምድር ላይ ካሉት ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ጋር ኪዳን እገባለሁ። 11 ከእንግዲህ ሕይወት ያለው ፍጡር ሁሉ በጥፋት ውሃ እንደማይጠፋ፣ ዳግመኛም ምድርን የሚያጠፋ ውሃ ከቶ እንደማይመጣ ከእናንተ ጋር ኪዳን እገባለሁ።” 12 እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፦ “በእኔና በእናንተ መካከል ከእናንተም ጋር ካሉ ሕያዋን ፍጡራን ሁሉ፣ ከሚመጣው ትውልድ ሁሉ ጋር፣ የማደርገው የኪዳኑ ምልክት ይህ ነው፤ 13 ቀስተ ደመናዬን በደመና ላይ አድርጋለሁ፤ ይህም በእኔና በምድር መካከል ለገባሁት ኪዳን ምልክት ይሆናል። 14 ደመናን በምድር ላይ በጋረድሁና ቀስቴም በደመና ላይ በሚታይበት ጊዜ ሁሉ 15 ከእናንተና ከሕያዋን ፍጡራን ሁሉ ጋር የገባሁትን ኪዳን አስባለሁ፤ ሕይወት ያለውንም ሁሉ ያጠፋ ዘንድ፣ ከእንግዲህ የጥፋት ውሃ ከቶ አይመጣም። 16 ቀስቱ በደመና ላይ ተገልጦ በማይበት ጊዜ ሁሉ በእኔና በምድር ላይ ባሉ ሕያዋን ፍጡራን መካከል ያለውን ዘላለማዊ ኪዳን አስባለሁ።” 17 ከዚያ በኋላም እግዚአብሔር ለኖኅ፦ “ይህ በእኔና በምድር ላይ በሚኖሩ ሕያዋን ሁሉ መካከል የገባሁት ኪዳን ምልክት ነው።” አለው። 18 ከመርከቧ የወጡትም የኖኅ ልጆች ሴም፣ ካምና ያፌት ነበር፤ ካም የከነዓን አባት ነው። 19 እነዚህ ሶስቱ የኖኅ ልጆች ሲሆኑ፣ በምድር ላይ የሚኖሩ ሕዝቦች ሁሉ የተገኙት ከነዚሁ ነው። 20 ኖኅ ገበሬ መሆን ጀመረ፣ ወይንንም ተከለ። 21 ከወይኑም ጠጅ ጠጥቶ ሰከረና በድንኳኑ ውስጥ እርቃኑን ተኛ። 22 የከንዓን አባት ካም የአባቱን ዕርቃነ ሥጋ አየ፤ ወደ ውጭም ወጥቶ ለሁለቱ ወንድሞቹ ነገራቸው። 23 ሴምና ያፌት ግን ልብስ ወስደው በትከሻቸው ላይ አደረጉና የአባታቸውን ዕርቃነ ሥጋ እንዳያዩ ፊታቸውን አዙረው የኋሊት በመሄድ የአባታቸውን ዕርቃነ ሥጋ ሸፈኑ። 24 ኖኅ ከወይን ጠጁ ስካር ሲነቃ ታናሽ ልጁ ያደረገበትን አወቀ። 25 ከዚህም የተነሣ፦ “ከነዓን የተረገመ ይሁን፤ ለወንድሞቹም አገልጋይ ይሁን።” አለ። 26 ደግሞም፦ “የሴም አምላክ የሆነው እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን፣ ከነዓንም የሴም አገልጋይ ይሁን። 27 እግዚአብሔር የያፌትን ግዛት ያስፋ፤ ያፌት በሴም ድንኳኖች ይኑር፤ ከነዓን የያፌት አገልጋይ ይሁን።” አለ። 28 ኖኅ ከጥፋት ውሃ በኋላ 350 ዓመት ኖረ። 29 ኖኅ በአጠቃላይ 950 ዓመት ኖሮ ሞተ።



Chapter 10

1 የኖኅ ልጆች የሴም፣ የካምና የያፌት ዝርያዎች የሚከተሉት ናቸው። ከጥፋት ውሃም በኋላ ልጆች ተወለዱላቸው። 2 የያፌት ልጆች፦ ጋሜር፣ ማጎግ፣ ማዴ፣ ያዋን፣ ቶቤል፣ ሞሳሕና ቴራስ ነበሩ። 3 የጋሜር ልጆች፦ አስከናዝ፣ ሪፋትና ቴርጋማ ነበሩ። 4 የያዋን ልጆች፦ ኤሊሳ፣ ተርሴስ፣ ኪቲምና ሮዳኢ ነበሩ። 5 ከእነዚህም በየነገዳቸው በየጎሳቸውና በየቋንቋቸው ተከፋፍለው በባሕር ዳርና በደሴቶች በየምድራቸው የሚኖሩ ሕዝቦች ወጡ። 6 የካም ልጆች፦ ኩሽ፣ ምጽራይም፣ ፉጥና ከነዓን ነበሩ። 7 የኩሽ ልጆች፦ ሳባ፣ ኤውላጥ፣ ሰብታ፣ ራዕማና ሰበቀታ ነበሩ። የራዕማ ልጆች፦ ሳባና ድዳን ነበሩ። 8 ኩሽ በምድር ላይ የመጀመሪያው ታላቅ ጦረኛ የነበረው የናምሩድ አባት ነበር። 9 እርሱም በእግዚአብሔር ፊት ብርቱ አዳኝ ነበር። ስለዚህም፣ “በእግዚአብሔር ፊት እንደ ናምሩድ ብርቱ አዳኝ” ይባል ነበር። 10 የግዛቱም የመጀመሪያ ከተሞች በሰናዖር ምድር የነበሩት፡- ባቢሎን፣ አሬክ፣ አርካድና ካልኔ ነበሩ። 11 ከዚያም ወደ አሦር ምድር ሄደና ነነዌን፣ ርሆቦትን፣ ካላሕን 12 እንዲሁም በነነዌና በካላሕ መካከል የነበረውን ታላቅ ከተማ ሬሴን የተባሉትን ከተሞች መሠረተ። 13 ምጽራይም የሎዳማውያን፣የዐናሚማውያን፣ የላህሚማውያን፣ የነፍታሌማውያን፣ 14 የፈተሩሲማውያንና ፍልስጥኤማውያን የተገኙባቸው የካስሎሂማውያንና የቀፍቶርማውያን አባት ነበር። 15 የከነዓንም የበኩር ልጅ ሲዶን ተከታዩም ሔት ይባሉ ነበር። 16 ሌሎቹም የከነዓን ዝርያዎች ኢያቡሳውያን፣ አሞራውያን፣ ጌርጌሳውያን፣ 17 ኤውያውያንን፣ ዓርቃውያን፣ ሲናውያን፣ 18 ኤርዋዳውያን፣ አርዋዳውያን፣ ደማራውያን፣ ሐማታውያን የሚባሉ ነበሩ። ከጊዜ በኋላ የከነዓን ጎሣዎች በየስፍራው ተሠራጩ። 19 የከነዓን ወሰን ከሲዶና አንሥቶ በጌራራ በኩል ገሞራን አዳማንና ሰቦይን ይዞ እስከ ላሣ ይዘልቃል። 20 እነዚህም በየጎሣቸውና በየቋንቋቸው በየምድራቸውና በየነገዳቸው ይኖሩ የነበሩ የካም ዝርያዎች ነበሩ። 21 ለያፌት ታላቅ ወንድም ለሴም ደግሞ ወንዶች ልጆች ተወለዱለት፤ እርሱም የዔቦር ልጆች ሁሉ ቅድመ አያት ነበር። 22 የሴም ልጆች ኤላም፣ አሦር፣ አርፋክስድ፣ ሉድ፣ አራም ነበሩ። 23 የአራም ልጆች ዑፅ፣ ሁል፣ ጌቴር፣ ሞሶሕ ነበሩ። 24 አርፋክስድ ሳላን ወለደ፤ ሳላም ኤቦርን ወለደ። 25 ዔቦርም ሁለት ወንዶች ልጆችን ወለደ። በዘመኑ ምድር ተከፍላ ስለነበር የአንደኛው ልጅ ስም ፍሌቅ ተባለ፤ ወንድሙም ዮቅጣን ተባለ። 26 ዮቅጣንም የአልሞዳድ፣ የሼሌፍ፥ የሐጸርማዌት፣ የዮራሕ፣ 27 የዐዶራም፣ የኢዛል፣ የዲቅላ፣ 28 የዖባል፣ የአቢማኤል፣ የሳባ፣ 29 የኦፊር፣ የሐዊላና የዮባብ አባት ነበር። እነዚህ ሁሉ የዮቅጣን ዝርያዎች ነበሩ። 30 መኖርያ ስፍራቸውም በስተምሥራቅ ባለው በተራራማው አገር ከሜሻ እስከ ስፋር ይደርስ ነበር። 31 እነዚህም በየጎሣቸውና በየቋንቋቸው በየምድራቸውና በየነገዳቸው ይኖሩ የነበሩ የሴም ዝርያዎች ነበሩ። 32 የኖኅ ወንዶች ልጆች ጎሣዎች እንደ ትውልዳቸው በየነገዳቸው እነዚህ ነበሩ። ከጥፋት ውሃ በኋላ ሕዝቦች በምድር ላይ የተሠራጩት ከእነዚሁ ነበር።



Chapter 11

1 በዚያ ዘመን መላው ዓለም የሚናገረውና የሚግባባው በአንድ ቋንቋ ነበር። 2 ወደ ምሥራቅ ሲጓዙ፣ በሰናዖር አንድ ሜዳማ ቦታ አግኝተው በዚያ ሰፈሩ። 3 እርስ በርሳቸውም፣ “ኑ፣ ጡብ እንሥራና እስከበቃው ድረስ በእሳት እንተኩሰው” ተባባሉ። በድንጋይ ፈንታ ጡብ ተጠቀሙ፤ ጡቡን እርስ በርስ ለማያያዝም ቅጥራን ተጠቀሙ። 4 ከዚያም፣ “ለስማችን መጠሪያ እንዲሆን ጫፉ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንሥራ። ያንን ካላደረግን በምድር ሁሉ ፊት መበታተናችን ነው” አሉ። 5 የአዳም ልጆች የሠሩትን ለማየት ያህዌ ወደ ከተማውና ወደ ግንቡ ወረደ። 6 ያህዌም፣ “አንድ ቋንቋ የሚናገሩ አንድ ሕዝብ በመሆናቸው ይህን ማድረግ ችለዋል! ከእንግዲህ ማድረግ የፈለጉትን ለማድረግ ምንም የሚያቅታቸው አይኖርም። 7 ኑ እንውረድ፤ አርስ በርስ እንዳይግባቡም ቋንቋቸውን እንደበላልቀው” አለ። 8 ስለዚህ ያህዌ ከዚያ ቦታ ወደ መላው ዓለም በታተናቸው፣ እነርሱም ከተማዋን መሥራት አቋረጡ። 9 በዚያ የዓለምን ቋንቋ ስለ ደበላለቀ የከተማዋ ስም ባቤል ተባለ። ከዚያም ያህዌ በመላው ዓለም በተናቸው። 10 የሴም ትውልድ ይህ ነው። የጥፋት ውሃ ከመጣ ሁለት ዓመት በኋላ ሴም መቶ ዓመት ሲሆነው አርፋድሰድን ወለደ። 11 አርፋድሰድን ከወለደ በኋላ ሴም አምስት መቶ ዓመት ኖረ። ሌሎች ወንዶች እና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 12 አርፋክሰድ በሰለሣ አምስት ዓመቱ ሰላን ወለደ፤ 13 ሰላን ከወለደ በኋላ አርፋክሰድ አራት መቶ ሦስት ዓመት ኖረ፤ እርሱም ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 14 ሳላ ሰላሣ ዓመት ሲሆነው ዔቦርን ወለደ፤ 15 ዔቦርን ከወለደ በኋላ ሳላ አራት መቶ ሦስት ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 16 ዔቦር አራት ዓመት ሲሆነው ፋሌቅን ወለደ፤ 17 ፋሌቅን ከወለደ በኋላ ዔቦር አራት መቶ ሰላሣ ዓመት ኖረ፤ እርሱም እንዲሁ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 18 ፋሌቅ ሰለሣ ዓመት ሲሆነው፣ ራግውን ወለደ፤ 19 ራግውን ከወለደ በኋላ ፋሌቅ ሁለት መቶ ዘጠኝ ዓመት ኖረ፤ እርሱም እንዲሁ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 20 ራግው ሰለሣ ሁለት ዓመት ሲሆነው፣ ሴሮሕን ወለደ፤ 21 ሴሮሕን ከወለደ በኋላ ራግው ሁለት ሞት ሰባት ዓመት ኖረ፤ እርሱም እንዲሁ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 22 ሴሮሕ ሰለሣ ዓመት ሲሆነው፣ ናኮርን ወለደ፤ 23 ናኮርን ከወለደ በኋላ ሴሮሕ ሁለት መቶ ዓመት ኖረ፤ እርሱም እንዲሁ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 24 ናኮር ሃያ ዘጠኝ ዓመት ሲሆነው ታራን ወለደ፤ 25 ታራን ከወለደ በኋላ ናኮር አንድ መቶ አሥራ ዘጠኝ ዓመት ኖረ፤ እርሱም እንዲሁ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆች ወለደ። 26 ታራ ሰባ ዓመት ሲሆነው አብራምን፣ ናኮርንና ሐራንን ወለደ። 27 የታራ ትውልድ ይህ ነው። ታራ፣ አብራምን፣ ናኮርንና ሐራን ወለደ። ሐራን ሎጥን ወለደ። 28 ሐራን አባቱ ታራ በሕይወት እያለ በተወለደበት ከተማ በከለዳውያን ዑር ሞተ። 29 አብራምና ናኮር ሁለቱም ሚስት አገቡ። የአብራም ሚስት ሦራ ስትባል፣ የናኮር ሚስት ደግሞ ሚልካ ትባል ነበር፤ ሚልካ የሐራን ልጅ ስትሆን፣ ሐራን የሚልካና የዮሳካ አባት ነበር። 30 ሦራ ምንም ልጅ ያልነበራት መካን ነበረች። 31 ታራ ልጁ አብራምን፣ የልጅ ልጁን ሎጥንና የአብራምን ሚስት ምራቱን ሦራን ይዞ ወደ ከነዓን ለመሄድ በከለዳውያን ምድር ከምትገኘው ዑር አብረው ወጡ። ሆኖም፣ ካራን በደረሱ ጊዜ በዚያ ተቀመጡ። 32 ታራ ሁለት መቶ አምስት ዓመት ኖሮ በካራን ሞተ።



Chapter 12

1 በዚህ ጊዜ ያህዌ አብራምን እንዲህ አለው፤ “አገርህን፣ ወገንህንና የአባትህን ቤተ ሰብ ትተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ፤ 2 ታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ፤ እባርክሃለሁ፤ ስምህን ገናና አደርገዋለሁ፤ ለሌሎችም በረከት አደርግሃለሁ። 3 የሚባርኩህን እባርካለሁ፤ የሚረግሙህንና የሚያዋርዱህን እረግማለሁ። በአንተ አማካይነት በምድር የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ ይባረካሉ።” 4 ስለዚህ አብራም ያህዌ እንዳዘዘው ወጣ፤ ሎጥም አብሮት ሄደ። አብራም ከካራን ተነሥቶ ሲሄድ፣ የሰባ አምስት ዓመት ሰው ነበር። 5 አብራም ሚስቱ ሦራን፣ የውንድሙ ልጅ ሎጥን አስከትሎ በካራን ያፈሩትን ሀብትና የነበራቸውን አገልጋዮች ይዞ በመጓዝ፣ ከነዓን ምድር ገቡ። 6 አብራም በሞሬ ያለው ግዙፍ የወርካ ዛፍ እስካለበት እስከ ሴኬም ዘልቆ ሄደ። በዚያ ዘመን ከነሻናውያን በዚህ ምድር ይኖሩ ነበር። 7 ያህዌ ለአብራም ተገልጦ፣ “ይህችን ምድር ለዘርህ እሰጣለሁ” አለው። ስለዚህ አብራም ለተገለጠለት ለያህዌ በዚያ መሠዊያ ሠራ። 8 ከዚያ በመነሣት ከቤቴል በስተ ምሥራቅ ወዳለው ተራራማ አገር ሄደ፤ ቤቴል በስተ ምዕራብ፣ ጋይ በስተ ምዕራብ ባለችበት ቦታ ድንኳኑን ተከለ። እዚያ ለያህዌ መሠዊያ ሠራ፤ የያህዌንም ስም ጠርቶ ጸለየ። 9 አብራም ከዚያ ተነሥቶ ወደ ኔጌብ መጓዙን ቀጠለ። 10 በዚያ ምድር ጽኑ ራብ ስለ ነበር አብራም እዚያ ጥቂት ጊዜ ለመቆየት ወደ ግብፅ ሄደ። 11 ግብፅ በመግባት ላይ እያለ አብራም ሚስቱ ሦራን እንዲህ አላት፤ “መቼም አንቺ ቆንጆ ሴት መሆንሽን አውቃለሁ። 12 ግብፃውያን ሲያዩሽ ‘ይህች ሚስቱ ናት’ ይላሉ፤ እኔን ይገድሉኛል፤ አንቺን ግን ይተዉሻል። 13 ስለዚህ በአንቺ ምክንያት ለእኔ መልካም እንዲሆልኝ ሕይወቴም እንዲተርፍ እኅቱ ነኝ’ በዪ አላት። 14 አብራም ወደ ግብፅ ሲገባ፣ ሦራ ምን ያህል ቆንጆ እንደ ሆነች ግብፃውያኑ አዩ። 15 የፈርሾን ሹማምንት ባዩአት ጊዜ እርሷን እያደነቁ ለፈርዖን ነገሩት፤ ወደ ቤተ መንግሥትም ተወሰደች። 16 በእርሷ ምክንያት ፈርኦን አብራምን በክብር አስተናገደው፤ በጎች፣ በሬዎች፣ ወንድ አህዮች ወንድና ሴት ባሪያዎች፣ ሴት አህዮችና ግመሎች ሰጠው። 17 በአብራም ሚስት በሦራ ምክንያት ያህዌ ፈርዖንና ቤተ ሰቡን በታላቅ መቅሠፍት መታ። 18 ፈርዖን አብራምን አስጠርቶ እንዲህ አለው፤ “ለመሆኑ ምን እያደረግህብኝ ነው? ሚስትህ መሆንዋን ለምን አልነገርከኝም? 19 ለምን እኅቴ ናት አልከኝ? እኅቴ ናት ስላልከኝ ሚስቴ ላደርጋት ነበር። አሁንም ሚስትህ እቻት፤ ይዘሃት ሂድ” 20 ከዚያም ፈርዖን አብራምን በተመለከተ ለባለሟሎቹ ትእዛዝ ሰጠ፤ እነርሱም አብራምን ከሚስቱና ከንብረቱ ሁሉ ጋር አሰናበቱት።



Chapter 13

1 ስለዚህ አብራም ሚስቱንና ያለውን ንብረት ሁሉ ይዞ ከግብፅ ወደ ኔጌብ ሄደ። ሎጥም ከእነርሱ ጋር ነበረ። 2 በዚህ ጊዜ አብራም በከብት፣ በብርና በወርቅ በልጽጎ ነበር። 3 ከኔጌብ ተነሥቶ እስከ ቤቴል ተጓዘ፤ ቀድሞ ድንኳን ተክሎበት ወደ ነበረው በቤቴልና በጋይ መካከል ወደ ነበረው ቦታ ደረሰ። 4 ይህ ቀድሞ መሠዊያ የሠራበት ቦታ ሲሆን በዚያ ያህዌን ጠራ። 5 ከአብራም ጋር ይጓዝ የነበረው ሎጥ የራሱ በጎች፣ ከብቶችና ድንኳኖች ነበሩት። 6 ሁለቱ አንድ ላይ ይኖሩ ስለ ነበር ስፍራው አልበቃቸውም፤ በዚህ ላይ ንብረታቸውም በጣም ብዙ ስለ ነበር አብረው መኖር አልቻሉም። 7 ይህም በመሆኑ በአብራምና በሎጥ እረኞች መካከል ጠብ ተፈጠረ። በዚያ ዘመን ከነኣናውያንና ፌርዛውያን በዚያው አገር ይኖሩ ነበር። 8 አብራም ሎጥን እንዲህ አልው፤ “በእኔና በአንተ፣ በእኔ እረኞችና በአንተ እረኞች መካከል ግጭት መኖር የለበትም፤ በዚህ ላይ ደግሞ ቤተ ሰብ ነን። 9 ይኸው እንደምታየው ምድሩ ሰፊ ነው፤ ብንለያይ ይሻላል። አንተ ግራውን ብትመርጥ፣ እኔ ወደ ቀኝ እሄዳለሁ፤ ወይም አንተ ቀኙን ብትመርጥ እኔ ወደ ግራ እሄዳለሁ። 10 ስለዚህ ሎጥ ዙሪያውን ሲመለከት እስከ ዞዓር ድረስ ያለው የዮርዳኖስ ረባዳ ሜዳ ሁሉ እንደ ያህዌ ገነት እንደ የግብፅ ምድር በጣም ለም ሆኖ አገኘው። እንዲህ የነበረው እግዚአብሔር ሰዶምና ገሞራን ከማጥፋቱ በፊት ነበር። 11 ሎጥ የዮርዳኖስን ረባዳ ሜዳ ሁሉ መርቶ ወደ ምሥራቅ ተጓዘ፤ በዚህ ሁኔታ ዘመዳሞቹ ተለያዩ። 12 አብራም መኖሪያውን በከነዓን ምድር አደረገ፤ ሎጥ ግን በረባዳው ሜዳ ባሉት ከተሞች መካከል ኖረ። እስከ ሰዶም ድረስ ባለው ቦታ ድንኳኖቹን ተከለ። 13 የሰዶም ሰዎች በጣም ዐመፀኞችና በያህዌም ፊት እጅግ ኀጢአተኞች ነበሩ። 14 ሎጥ ከእርሱ ከተለየው በኋላ ያህዌ አብራምን እንዲህ አለው፤ “ካለህበት ቦታ ወደ ሰሜን፣ ወደ ደቡብ፣ ወደ ምሥራቅና ምዕራብ ተመልከት። 15 ይህን የምታየውን ምድር ሁሉ ለአንተና ለዘርህ ለዘላለም እሰጣለሁ። 16 ዘርህን እንደ ምድር ትቢያ አበዛዋለሁ፤ የምድር ትቢያ ሊቆጠር እንደማይቻል ሁሉ የአንተም ዘር ሊቆጠር አይችልም። 17 እንግዲህ ምድሪቱን ስለምስጥህ ተነሣና በርዝመትና በስፋቱ ተመላለሰባት።” 18 ስለዚህ አብራም ድንኳኑን ነቀለና በኬብሮን ወዳሉት የመምሬ ወርካ ዛፎች መጥቶ ኖረ፤ እዚያም ለያህዌ መሠዊያ ሠራ።



Chapter 14

1 አምራፌል የሰናዖር ንጉሥ፣ አርዮክ የአላሳር ንጉሥ፣ ከሎደጎምር የኤላም ንጉሥ፣ ተድዓል የጎይም ንጉሥ፣ 2 በነበሩበት ዘመን፤ ከሰዶም ንጉሥ በላ፣ ከጎሞራ ንጉሥ ከብርሳ፣ ከአዳማ ንጉሥ ከሰነአብ፣ ከሰቦይ ንጉሥ ከሰሜበር፣ እንዲሁም ዞዓር ከተባለች ከቤላ ንጉሥ ጋር ለመዋጋት ወጡ። 3 እነዚህ የኋለኞቹ አምስት ነገሥታት የጨው ባሕር እየተባለች በምትጠራው በሲዶም ሸለቆ ተሰበሰቡ። 4 እነርሱም አሥራ ሁለት ዓመት ለኮሎዶጎምር ተገዙ፤ በአሥራ ሦስተኛው ዓመት ግን ዐመፁ። 5 በአሥራ አራተኛው ዓመት ከሎዶጎምርና ከእርሱም ጋር የነበሩት ነገሥታት መጥተው ራፋይምን፣ በአስታሮት ቃርናይምን፣ በካም ዙዚምን፣ በሴዊ ኑሚምን፣ በሸቮት ኢምንን፣ 6 የሖር ሰዎችንም በተራራማው አገር በሴይ በረሐማ አጠገብ እስካለው እስከ አልፋራን ድረስ ድል አደረጋቸው። 7 ከዚያም ተመልሰው ዓይንሚስፓጥ ወደሚባለው ወደ ቃዴስ መጡ፤ የአማሌዋውያንና በሐሴስ ታማር ይኖሩ የነበሩትን የአሞራውያን ግዛት በሙሉ ድል አድርገው ያዙ። 8 ከዚያም የሶዶም፣ የገሞራ፣ የአዳማ፣ የሰቦይ እንዲሁም ዞዓር የተባለችው የቤላ ነገሥታት ወደ ሲዶም ሸለቆ ሄደው ለጦርነት ተዘጋጁ። 9 እነዚህ አምስቱ በኤላም ንጉሥ በኮሎዶጎምር፣ በጎይም ንጉስ በቲድዓል፣ በሰናዖር ንጉሥ በአምራፌል፣ በአላሶር ንጉሥ በአርዮክ በእነዚህ ላይ ዘመቱባቸው። 10 በሲዲም ሸለቆ ብዙ የቅጥራን ጉድጓዶች ነበሩ፤ የሰዶምና የጎመራ ነገሥታት ሲሸሹ ከሰዎቻቸው አንዳንዶቹ በእነዚህ ጉድጓዶች ውስጥ ወደቁ። የተረፉትም ወደ ተራሮች ሸሹ። 11 አራቱ ነገሥታትም በሰዶምና በጎሞራ ያገኙትን ሀብትና ምግብ ሁሉ ዘርፈው ሄዱ። 12 በሰዶም ይኖር የነበረውን የአብርሃምን ወንድም ልጅ ሎጥንና የነበረውን ንብረት ሁሉ ይዘው ሄዱ። 13 ከዚያ ያመለጠ አንድ ሰው መጥቶ ለዕብራዊው ለአብራም ነገረው። በዚያ ጊዜ ይኖር የነበረው የአስኮና የእውናን ወንድም በነበረው በአሞራዊው መምሬ ዋርካ ዛፎች አጠገብ ነበር፤ እነዚህ ሁሉ የአብራም አጋሮች ነበር። 14 ጠላት ዘመዶቹን ማርኮ መውሰዱን አብራም ሲሰማ በቤቱ ተወልደው ያደጉ ሦስት መቶ አሥራ ስምንት ሰዎች ይዞ እስከ ዳን ድረስ ተከታተሏቸው። 15 አብራም ጠላቶቹን ለማጥቃት ሰራዊቱን ሌሊቱን በቡድን በቡድን ከፋፍሎ ከደማስቆ በስተ ሰሜን እስከሚገኘው እስከ ሖባ ድረስ አሳደዳቸው። 16 ጠላት የማረከውን በሙሉ አስጣለ፤ ዘመዱ ሎጥንና ንብረቱን፣ እንዲሁም ሴቶቹንና ሌሎች ሰዎችን አስመለሰ። 17 አብራም የኮሎዶጎምርንና ከእርሱ ጋር የነበሩ ነገሥታትን ድል አድርጎ ሲመለስ የሰዶም ንጉሥ የንጉሥ ሸለቆ ተብሎ በሚጠራው በሴዊ ሸለቆ ሊቀበለው ወጣ። 18 የሰሌም ንጉሥ መልከጼዴቅ እንጀራና ወይን ጠጅ ይዞ መጣ። እርሱ የልዑል አምላክ ካህን ነበር። 19 አብራምም እንዲህ በማለት ባረከው፣ “ሰማይና ምድርን የፈጠረ ልዑል እግዚአብሔር አብራምን ይባርክ። 20 ጠላቶችህን በእጅህ አሳልፎ የሰጠ ልዑል እግዚአብሔር ይባረክ።” አብራምም ይዞት ከነበረው ሁሉ አንድ አሥረኛውን ሰጠው። 21 የሰዶም ንጉሥ አብራምን፣ “ሰዎቹን ለእኔ ስጠኝ፤ ንብረቱን ግን ለራስህ አስቀር” አለው። 22 አብራምም ለሰዶም ንጉሥ እንዲህ አለው፤ “ከአንተ ብጣሽ ክርም ሆነ የጫማ ማሰሪያ እንኳ ቢሆን፣ 23 ደግሞም ‘አብራምን ባለጸጋ አደረግሁት’ እንዳትል የአንተ ከሆነ ምንም ነገር እንዳልወስድ ሰማይና ምድርን ወደ ፈጠረ አምላክ ወደ ያህዌ እጄን አንሥቻለሁ። 24 አብረውኝ ያሉት ሰዎች ከበሉትና የእነርሱ ድርሻ ከሆነው በቀር ምንም ነገር አልወስድም። አውናን፣ ኤስኩልና መምሬ ድርሻቸውን ይውሰዱ።”



Chapter 15

1 ከዚህ በኋላ የያህዌ ቃል እንዲህ ሲል ወደ አብራም መጣ፤ “አብራም ሆይ፣ አትፍራ፤ እኔ ለአንተ ጋሻህ ነኝ፤ ታላቅ ሽልማትህም እኔው ነን።” 2 አብራምም፣ “ጌታ ያህዌ ሆይ፣ እኔ ልጅ የለኝም፤ የቤት ወራሽ የሚሆነው የደማስቆው ሰው ኤሊዔዘር ነው፤ ታዲያ አንተ ለእኔ የምትሰጠኝ ምንድን ነው?” አለ። 3 በመቀጠልም አብራም “አንተ ልጅ እስካልሰጠኸኝ ድረስ፣ ከቤቴ አገልጋይ አንዱ ወራሼ መሆኑ አይቀርም” አለ። 4 በዚህ ጊዜ የያህዌ ቃል እንዲህ ሲል ወደ እርሱ መጣ፤ “ይህ ሰው ወራሽህ አይሆንም፤ ይልቁንም ወራሽህ የሚሆነው ከአብራክህ የሚከፈል የራስህ ልጅ ይሆናል።” 5 ከዚያም ወደ ውጭ አወጣውና እንዲህ አለው፤ “ቀና ብለህ ወደ ሰማይ ተመልከት፤ መቍጠር ከቻልህ ከዋክብቱን ቍጠር። ዘርህም እንዲሁ ይበዛል።” 6 አብራም ያህዌን አመነ፤ እርሱም ጽድቅ አድርጎ ቆጠረለት። 7 እንዲህም አለው፤ “ይህችን ምድር እንድትወርስ ልሰጥህ ከከለዳውያን ምድር ከዑር ያወጣሁህ እኔ ያህዌ ነኝ።” 8 አብራምም፣ “ጌታ ያህዌ ሆይ፣ ይህችን ምድር እንደምወርስ እንዴት አውቃለሁ?” አለ። 9 በዚህ ጊዜ፣ “እያንዳንዳቸው ሦስት ዓመት የሆናቸው አንዲት ጊደር፣ አንዲት ፍየልና አንድ በግ እንዲሁም ዋኖስና አንድ ርግብ አቅርብልኝ” አለው። 10 እርሱም እነዚህን ሁሉ አቀረበለት፤ ቆርጦም ሁለት ቦታ ከከፈላቸው በኋላ እያንዳንዱን ክፍል በሌላው ወገን ትይዩ አስቀመጣቸው፤ ወፎቹን ግን አልከፈላቸውም። 11 አሞሮች ሥጋውን ለመብላት ወረዱ፤ አብራምም አባረራቸው። 12 ፀሓይ ልትጠልቅ ስትል አብራም ከባድ እንቅልፍ ወሰደው፤ የሚያስፈራም ድቅድቅ ጨለማም መጣበት። 13 በዚህ ጊዜ ያህዌ አብራምን እንዲህ አለው፤ “ዘሮችህ የራሳቸው ባልሆነ ምድር ባዕድ እንደሚሆኑና እዚያ ለአራቶ መቶ ዓመት በባርነት እንደሚኖሩ በእርግጥ ዕወቅ። 14 እኔም ባሪያዎች ባደረጓቸው ሕዝብ እፈርዳለሁ፤ በኋላም ብዙ ሀብት ይዘው ይወጣሉ። 15 አንተ ግን በሰላም ወደ አባቶችህ ትሄዳለህ፤ ዕድሜም ጠግበህ ትቀበራለህ። 16 በአራተኛውም ትውልድ እንደ ገና ወደዚህ ይመጣሉ፤ ምክንያቱም የአሞራውያን ኀጢአት ጽዋው ገና አልሞላም።” 17 ፀሓይ ገብታ ከጨለመ በኋላ የምድጃ ጢስና የሚንበለበል ፋና በተቆራረጡት ሥጋዎች መካከል አለፈ። 18 በዚያን ቀን ያህዌ እንዲህ በማለት ከአብራም ጋር ኪዳን አደረገ፤ “ከግብፅ ወንዝ ጀምሮ እስከ ታላቁ ወንዝ ኤፍራጥስ ድረስ ያለውን ምድር ለዘርህ እሰጣለሁ፤ 19 የምሰጣቸውም የቄናውያንን፣ የቄንፌዛውያንን፣ የቃድሞናውያንን፣ 20 የኬጢያውያንን፣ የፌርዛውያንን፣ የራፋይምን፣ 21 የአሞራውያንን፣ የከነዓናውያን፣ የጌርሳውያንንና የኢያቡሳውያን ምድር ነው።”



Chapter 16

1 የአብራም ሚስት ሦራ ልጅ አልወለደችለትም ነበር፤ ነገር ግን አጋር የምትባል ግብፃዊት አገልጋይ ነበረቻት። 2 አብራምንም፣ "ያህዌ ልጅ እንዳልወደልድ አድርጎኛል። ምናልባት በእርሷ በኩል ልጅ አገኝ ይሆናልና ክአገልጋዬ ጋር ተኛ" አለችው። አብራም ሦራ በነገረችው ተስማማ። 3 የአብራም ሚስት ሦራ ግብፃዊት አገልጋይዋ ሚስት እንድትሆነው ለአብራም የሰጠችው አብራም በከነዓን ምድር አሥር ዓመት ከኖረ በኋላ ነበር። 4 አብራም ክአጋር ግን'ኡንት አደረገ እርሷም ፀነሰች። አጋር መፅነሷን ባወቀች ጊዜ እመቤቷን በንቀት ማየት ጀመረች። 5 በዚህ ጊዜ ሦራ አብራምን፣ "ይህ በደል የደረሰብኝ በአንተ ምክንያት ነው። ኅቅፍህ ውስጥ እንድትሆን አገልጋዬን ሰጠሁ፤ እርሷ ግን መፅነሷን ስታውቅ እኔን መናቅ ጀመረች። ያህዌ በእኔና በአንተ መካከ ይፍረድ" አለችው። 6 አብራምም መልሶ ሦራን፣ "አገልጋይሽ እኮ በእጅሽ ውስጥ ናት እርሷ ላይ የፈለግሽውን ማድረግ ትችያልለሽ" አላት። ስለዚህ ሦራ ስላሠቃየቻት፣ አጋር ከቤት ጠፍታ ሄደች። 7 የያህዌ መልአክ አጋርን ምድረ በዳ ውስጥ በነበረ አንድ ምንጭ አጠገብ አገኛት፤ ያ ምንጭ ወደ ሱር በሚወስደው መንገድ ላይ ነበር። 8 መልአኩም፣ "የሦራ አገልጋይ አጋር ሆይ፣ ከየት መጣሽ ወዴትስ እየሄድሽ ነው?" አላት። እርሷም፣ "ከእመቤቴ ከሦራ ኮብልዬ እየሄድሁ ነው" አለችው። 9 የያህዌ መልአክ፣ "ወደ እመቤትሽ ተመለዒ፤ ራስሽንም ለሥልጣንዋ አስገዢ" አላት። 10 ከዚያም የያህዌ መልአክ፣ "ዘርሽን እጅግ አበዛዋለሁ፤ ከበምዛቱም የተነሣ ሊቆጠር አይቻልም" አላት። 11 የያህዌም መልአክ በተጨማሪ እንዲህ አላት፤ "እነሆ ፀንሰሻል ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፤ ያህዌ ችግርሽን ሰምቷልና ስሙን እስማኤል ትዪዋለሽ። 12 እርሱ እንደ ዱር አህያ ይሆናል። ከሰው ሁሉ ጋር ይጣላል፤ ሰው ሁሉም ከእርሱ ጋር ይጣላል፤ ከወንድሞቹ ሁሉ ተነጥሎ ይኖራል።" 13 እርሷም ይሚያናግራትን ያህዌን፣ "አንተኮ እኔን የምታይ አምላክ ነህ"በማለት ጠራችው፤ ምክንያቱም፥ "እርሱ እኔን እንዳየ ሁሉ እኔም እርሱን አየው ይሆን?" ብላ ነበር። 14 ስለዚህ ያ ምንጭ ብኤርልያህሮኢ ተባለ፤ የሚገኘው በቃዴስና በባሬድ መካከ ልነው። 15 አጋር ለአብራም ወድን ልጅ ወለደችለው፤ አብራምም አጋር የወለደችለትን ልጅ እስማኤል ብሎ ጠራው። 16 አጋር እስማኤልን በወለደች ጊዜ አብራም ሰማንያ ስድስት ዓመት ሆኖት ነበር።



Chapter 17

1 አብራም የዘጠና ዘጠኝ ዓመት ሰው እያለ ያህዌ ተገለጠለትና እንዲህ አለው፤ "እኔ ሁሉን ቻይ አምላክ ነኝ፤ በፊቴ ተመላለስ ነቀፋም አይኑርብህ። 2 በእኔና በአንተ መካከል የተደረገውን ኪዳን አጸናለሁ፤ አንተንም እጅግ አበዛሃለሁ።" 3 አብራም በግንባሩ መሬት ላይ ተደፋ፤ እግዚአበሔርም እንዲ አለው፤ 4 "እነሆ ኪዳኔ ክአንተ ጋር ነው። የብዙ ሕዝብ አባት አደርግሃለሁ። 5 ከእንግዲህ ስምህ አብራም መባል የለበትም፤ ስምህ አብርሃም መባል እለበት፤ ምክንያቱም የብዙ ሕዝብ አባት አድርጌሃለሁ። 6 እጅግ አበዛሃለሁ፣ ሕዝቦች ክአንተ ይገኛሉ፤ ነገሥታትም ክአንተ ይወጣሉ። 7 በእኔና በአንተ፣ ክአንተም በኋላ ከዘርህ ጋር ኪዳኔን እመሠርታለሁ፤ ለአንተ ከአንተም በኋላ ለዘርህ በዘላለም ኪዳን አምላክ እሆናችኋለሁ። 8 ለአንተና ከአንተም በኋላ ለዘርህ ይህች አሁን የምትኖርባትን የከነዓንን ምድር በሙሉ ለዘላለም ርስት አድርጌ እሰጣላለሁ፤ አምላካቸውም እሆናለሁ።" 9 ከዚያም እግዚአብሔር አብርሃምን፣ "በአንተም በኩል፣ አንተና ከአንተ በኋላ የሚመጣው ዘርህ ከትውልድ እስከ ትውልድ ኪዳኔን መጠበቅ አለባችሁ። 10 በእኔና በአንተ መካከል ከአንተም በኋላ በእኔና በዘርህ መካከል መጠበቅ ያለባችሁ ኪዳኔ ይህ ነው፤ በመካከላችሁ ያለ ወንድ ሁሉ ይገረዝ። 11 እናንተ ሸለፈታችሁን ትገረዛላችሁ፤ ይህም በእናንተ መካከል ያለው ኪዳን ምልክት ይሆናል። 12 በመካከላችሁ ያለው ማንኛውም ስምንት ዓመት የሞላው ወንድ የሚመጣው ትውልድ ሁሉ ይገረዝ። ይህ በቤትህ የተወለደውን በገንዘብህ የተገዛውን ሁሉ ይጨምራል። 13 ቤትህ ውስጥ የተወለደና በገንዘብህ የገዛኸው መገረዝ አለባቸው። ስለሆነም ኪዳኔ በዘላለም ኪዳን ሥጋችሁ ላይ ይሆናል። 14 ሸለፈቱን ያልተገረዘ ማንኛውም ወንድ ኪዳኔን አፍርሷልና ከወገኖቹ ይወገድ።" 15 እግዚአብሔር አብርሃምን እንዲህ አለው፤ "ሚስትህ ሦራን ክአንግዲህ ሥራ እንጂ ሦራ ብለህ አትጥራት። 16 እባርክሃለሁ፤ ከእርሷ ወንድ ልጅ እሰጥሃለሁ። እባርካታለሁ። እርሷም የብዙ ሕዝብ እናት ትሆናልች፤ የሕዝቦችም ነገሥታት ክአርሷ ይወጣሉ። 17 በዚህ ጊዜ አብርሃም በግንባሩ መሬት ላይ ተደፍቶ እየሳቀ በሉ እንዲህ አለ፤ "ለመሆኑ የመቶ ዓመት ሽማግሌ ልጅ መውልደድ ይችላል? የዘጠና ዓመቷ አሮጊት ሥራስ ብትሆን ልጅ መውለድ ይሆንላታል?" 18 አብርሃም እግዚአብሔርን፣ "ይልቅ፣ እስማኤልን ብቻ ባኖርህልኝ!" አለ። 19 እግዚአብሔርም፣ "እንደዚያ አይደለም፤ ሚስትህ ሥራ ወንድ ልጅ ትወልድልሃለች፤ ስሙንም ይስሐቅ ብለህ ትጠራዋለህ። የዘላለም ኪዳኔን ከእርሱ ጋር፣ ከእርሱም በኋላ ከዘሩ ጋር እመጸርታለሁ። 20 እስማኤልን በተመለከተም ልምናህን ሰምቻለሁ። እነሆ እርሱንም እባርከዋለሁ፤ ፍሬያማም አደርገዋለሁ፤ እጅግም አበዛዋለሁ። የአሥራ ሁለት ነገዶች አባት ይሆናል፤ ታላቅ ሕዝብ እንዲሆንም አደርጋለሁ። 21 ኪዳኔን ግን፣ የዛሬ ዓመት በዚህ ጊዜ ሣራ ከምትወልድህል ከይስሐቅ ጋር እመሠርታለሁ።" 22 ከእርሱ ጋር መነጋገሩን ከጨረሰ በኋላ እግዚአብሔር ወደ ላይ ወጣ። 23 በዚያኑ ዕለት አብርሃም ልጁ ይስሐቅን፣ በቤቱ ውስጥ የተወለዱትን በሙሉ፣ በገንዘቡ የገዛቸውን ሁሉ፣ ቤቱ ውስጥ ያለ ማንኛውንም ወንድ ሁሉ እግዚአብሔር በነገረው መሠረት ገረዛቸው። 24 አብርሃም በተገረዘ ጊዜ እድሜው ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ነበር። 25 ልጁም እስማኤል በተገረዘ ጊዜ እድሜው አሥራ ሦስት ነበር። 26 በዚያው ቀን አብርሃምና ልጁ እስማኤልም ተገረዙ። 27 ቤቱ ውስጥ የተወለዱትን፣ ከውጭ በገንዘብ የተገዙትን ጨምሮ ቤቱ ውስጥ የነበሩ ወንዶች ሁሉ ከእርሱ ጋር ተገረዙ።



Chapter 18

1 ቀኑ በጣም ሞቃት በሆነ ጊዜ አብርሃም በመምሬ ወርካ ዛፎች አቅራቢይ ኣድንኳኑ ደጃፍ ተቀምጦ እያለ ያህዌ ተገለጥለት። 2 እርሱም ቀና ብሎ ሦስት ሰዎች ፊት ለፊቱ ቆመው አየ። ባያቸውም ጊዜ ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ፈጥኖ ወደ እነርሱ ሄዶ፣ ወደ መሬት ዝቅ ብሎም እጅ ነሣ። 3 አብርሃም እንዲህ አለ፤ "ጌታዬ፣ በፊትህ ሞገስ አግኝቼ ከሆነ፣ ባሪያህን አልፈህ አትሂድ። 4 ጥቂት ውሃ ትምጣላችሁና እግራችሁን ታጠቡ፤ ከዚያም ዛፉ ሥር ዐረፍ በሉ። 5 ወደ እኔ ወዳገልጋያችሁ ከመጣችሁ የደከመ ሰውነታችሁ እንዲበረታ እስቲ ጥቂት እህል ላምጣላችሁና ብሉ፤ ከዚያ ጕዞአችሁን ትቀጥላላችሁ።" እነርሱም. "እንዳልኸው አድርግ" አሉት። 6 ያኔውኑ አብርሃም በፍጥነት ሣራ ወደ ነበረችበት ድንኳን ገብቶ፣ "ቶሎ ብለሽ ሦስት መስፈሪያ ስልቅ ዱቄት አቡኪና ቂጣ ጋግሪ" አላት። 7 ከዚያም ወደ መንጋው በፍጥነት ሄዶ አንድ ፍርጥም ያለ ሥጋው ግን ገር የሆነ ጥጃ መረጠና ለአገልጋዩ ሰጠው፤ እርሱም በአስቸኳይ አደረሰው። 8 አብርሃምም እግሮ፣ ወተትና የተዘጋጀውን የጥጃ ሥጋ አቀበላቸው፤ እነርሱ እየበሉ እያለ እርሱ ዛፉ ሥር አጠገባቸው ቆሞ ነበር። 9 እነርሱም እንዲህ አሉት፤ "ሚስትህ ሥራ የታለች?" እርሱም፣ "ድንኳን ውስጥ ናት" አለ። 10 እነርሱም፣ "የዛሬ ዓመት በፀደይ ወቅት ልክ በዚሁ ጊዜ በእርግጥ ተመልሼ እመጣለሁ፤ ሚስትህ ሥራ ልጅ ትወልዳለች" አለ። ሥራ ከጀርባ በነበረው ድንኳን ደጃፍ ሆና ታዳምጥ ነበር። 11 በዚህ ጊዜ አብርሃምና ሥራ በጣም አርጅተው ነበር፤ ሥራማ ልጅ የመውለጃ ጊዜ አልፎባት ነበር። 12 ስለዚህ ሣራ በልቧ፣ "ይህን ያህል ካረጀሁና ጌታዬም ከደከመ በኋላ በዚህ ነገር መደሰት ይሆንልኛልን?" ብላ ሳቀች። 13 ያህዌ አብርሃምን እንዲህ አለው፤ "ካረጀሁ በኋላ እንዴት አድርጌ ልጅ እወልዳለሁ ስትል ሣራ የሳቀችው ለምንድን ነው? 14 ለመሆኑ ለያህዌ የሚሳነው ነገር አለ? እኔ በወሰንሁት የፀደይ ወቅት ወደ እናንተ እመለሳለህ፤ በሚመጣው ዓመት በዚህ ጊዜ ሥራ ወንድ ልጅ ትወልዳለች።" 15 ሣራ ግን ፈርታ ስል ነበር፣ "ኧረ እልሳቅሁም" በማለት ካደች። እርሱም፣ "የለም፤ ስቀሻል እንጂ" አላት። 16 ሰዎቹ ለመሄድ ሲነሡ ቁልቁል ወደ ሰዶም ተመለከቱ። አብርሃምም ሊሸኛቸው ከእነርሱ ጋር ሄደ። 17 በዚህ ጊዜ ያህዌ እንዲህ አለ፤ "እኔ የማደርገውን ክአብርሃም መደበቅ አለብኝን? 18 አብርሃም በእርግጥ ታላቅና ብርቱ ሕዝብ ይህሆናል፤ የምድር ሕዝቦችም ሁሉ በእርሱ ይባረካሉ። 19 ትክክለኛና ቀና የሆነውን በማድረግ የያህዌን መንገድ እንዲጠብቁ ልጆቹንና ከእርሱ በኋላ ቤተ ሰቡን እንዲያስተምር እኔ አብርሃምን መርጬዋለሁ፤ ይኸውም ለአብርሃም የነገረውን ሁሉ ያህዌ እንዲፈጽምለት ነው።" 20 ደግሞም እግዚአብሔር እንዲህ አለ፤ "በሰዶምና በገሞራ ላይ የሚሰማው ክስ በጣም ስለ በዛ፣ ኀጢአታቸውም በጣም ትልቅ ስል ሆነ፤ 21 ወደ እኔ የመጡ ክሶች ምን ያህል እውነት መሆናቸውን ለማየት ወደዚያ እወርዳለሁ፤ እንደዚይ ካልሆነም አውቃለሁ።" 22 ሰዎቹም ፊታቸውን ወደ ሰዶም አቅንተው ሄዱ፤ አብርሃም ግን ያህዌ ፊት እንደ ቆመ ነበር። 23 አብርሃም ወደ እርሱ ቀረብ ብሎ፣ "በእርግጥ ጻድቁን ከኀጢአተኛው ጋር ታጠፋለህን? 24 ምናልባት በከተማዋ ሃምሳ ጻድቃን ቢገኙስ? እዚያ ባሉ ጻድቃን ስትል ከተማዋን ሳታድን ታጠፋታለህን? 25 ጻድቁን ከኀጢአተኛው ጋር በመግደል፣ ኀጢአተኛ ላይ የደረሰው በእርሱም እንዲደርስ ማድረግን የመሰለ ንገር ከአንተ ይራቅ! እንዲህ ያለው ከአንተ ይራቅ! የምድር ሁሉ ዳኛ እውነተኛ ጻድቅ የሆነውን አያደርግምን? 26 ያህዌም እንዲህ አለ፤ "በሰዶም ከተማ ውስጥ ሃምሳ ጻድቃን ካገኘሁ ፣ ለእነርሱ ስል ያንን ቦታ እምራለሁ።" 27 አብርሃምም መልሶ እንዲህ አለ፤ "እኔ ትቢያና ዐመድ ሆኜ ሳለሁ ከጌታዬ ጋር ለመናገር አንዴ ደፍሬአለሁ፤ 28 ለመሆኑ ከአምሳዎቹ ጻድቃን አምስት ቢጎድሉ፣ በጎደሉት አምስቱ ምክንያት ከተማዋን በሙሉ ታጠፋለህን?" እርሱም፣ "እዚያ አርባ አምስ ጻድቃንካገኘሁ አላጠፋትም" አለ። 29 አብርሃምም እንደ ገና፣ "ምናልባት አርባ ጻድቃን ቢገኙስ?" እለ፤ እርሱም፣ "ለአርባዎቹ ስል አላደርገውም" እለ። 30 አብርሃምም፣ "እባክህን ጌታዬ ይህን ያህል በመናገሬ አትቆጣኝ። እንደው ምናልባት ሰለሣ ቢገኙስ" አለ። እርሱም መልሶ፣ "ሰላሣ ጻድቃን ካገኘሁ አላደርገውም" በማለት መለሰ። 31 አብርሃምም፣ "መቼም አንዴ ከጌታዬ ጋር መናገር ጀምሬአለሁ! እንደው ምናልባት ሃያ ቢገኙስ" አለ። እርሱም መልሶ፥ "ለሃያዎቹ ስል አላደርገውም" አለ። 32 በመጨረሻም እንዲህ አለ፤ "እባክህ ጌታዬ አትቆጣኝ፤ አንዴ ብቻ ልናገር፤ ምናልባት አሥር ቢገኙስ። እርሱም፣ "ለአሥሩ፣ ሲል አላጠፋትም" አለ። 33 ከአብርሃም ጋር መነጋገሩን እንደ ጨረሰ ያህዌ ሄደ፤ አብርሃምም ወደ ቤቱ ተመለሰ።



Chapter 19

1 ሁለቱ መላእክት ምሽት ላይ ወደ ሰዶም መጡ፤ በሰዶም ከተማ መግቢያበር ላይ ተቀምጦ ነበር። ሎጥ ሲያያቸው ሊቀበላቸው ተነሣ፤ በግንባሩም መሬት ላይ ተደፋ። 2 እርሱም፣ "እባካችሁ ጌቶቼ ወደ እኔ ወደ ባሪያችሁ ቤት ጎራ በሉ፤ እግራችሁን ታጠቡ፤ ሌሊቱንም ከእኛ ጋር አሳልፉ፤ ከዚያ ጧት በማለዳ ተነሥታችሁ ጕዞአችሁን ትቀጥላላችሁ።" እነርሱም፣ "የለም፤ እዚሁ አደባባዩ ላይ እናድራለን" አሉት። 3 ሎጥ ግን አጥብቆ ስለ ለመናቸው እርሱ ቤት ለማደር አብረውት ገቡ። ከዚያም ቂጣ ጋግሮ አቀረበላቸው፤ እነርሱም በሉ። 4 ሆኖም፣ ገና ከመተኛታቸው በፊት የሰዶም ከተማ ነዋሪዎች የሆኑ ወጣቶችና ሽማግሌዎች ከየአካባቢው መጥተው ቤቱን ከበቡት። 5 ሎጥን በመጣራት፣ "በዚህ ምሽት ወደ ቤትህ የመጡ ሰዎች የታሉ? ሩካቤ ሥጋ እንድንፈጽምባቸው ወደ ውጭ አውጣልን" አሉት። 6 ሎጥ ሊያነጋግራቸው ወደ ውጭ ወጣ መዝጊያውን ከበስተ ኋላው ዘጋ። 7 እንዲህም አለ፤ "ወንድሞቼ እንዲህ ያለ ክፉ ነገር እንዳታደርጉ እለምናችሏለሁ። 8 ከወንድ ጋር ተኝተው የማያውቁ ሁለት ሴቶች ልጆች አሉኝ፤ እነርሱን ላውጣላችሁና የወደዳችሁትን አድርጉባቸው። በእነዚህ ሰዎች ላይ ግን ምንም ነገር አታድርጉባቸው፤ እኔን ብለው ወደ ቤቴ ተብተዋልና።" 9 እነርሱ ግን፣ "ዞር በል!" ይኸ ሰውዬ ስደተኛ ሆኖ እዚህ ለመኖር መጣ፤ ደግሞ ዳኛ ሆነብን! ይልቁ በእነርሱ ላይ ካሰብነው የከፋ እንዳይደርስብህ ዘወር በልልን" አሉት ሎጥንም እየገፈታተሩ የበሩን መዝጊያ ለመስበር ተቃርበው ነበር። 10 ሰዎቹ እጃቸውን ዘርግተው ሎጥን ወደ ቤት አስገቡትና በሩን ዘጉ። 11 ከቤቱ ውጪ የነበሩትን ውጣቶችንም ሆን ሽማግሌዎችን ግን የሎጥ እንግዶች ዐይናቸውን አሳወሩአቸው፤ እነርሱም በሩን ለማግኘት ይደነባበሩ ጀመር። 12 ከዚያም ሰዎቹ ሎጥን እንዲህ አሉት፤ "በከተማዋ የሚኖሩ የአንተ የሆኑ ሰዎች አሉህ? ወንዶችና ሴቶች ልጆችህን፣ የወንዶች ልጆችህን ሚስቶች፣ የሴቶች ልጆችህን ባሎችና ሌሎች ዘመዶችህን ሁሉ ከዚህ አውጣ። 13 ምክንያቱም ይህን ቦታ ልናጠፋ ነው፤ በያህዌ ፊት ከተማዋ ላይ የሚቀርቡ ክሶች በጣም እየጮኹ በመሆናቸው እንድናጠፋት እርሱ ልኮናል።" 14 ሎጥ ከቤቱ ወጥቶ የሴት ልጆቹን ባሎች፣ የሴት ልጆቹን እጮኞች፣ "ቶሎ ከዚህ ቦታ ውጡ፤ ያህዌ ከተማዋን ሊያጠፋ ነው" አላቸው። የሴት ልጆቹ ባሎች ግን የሚቀልድ መሰላቸው። 15 ሲነጋጋም መላእክቱ ሎጥኝ፣ "ከተተማዋ ላይ በሚመጣው ቅጣት አብራችሁ እንዳትጠፉ ሚስትህንና ሁለቱ ሴት ልጆችህን ይዘህ ከዚህ ቦታ በፍጥነት ውጣ" እያሉ አቻኮሉት። 16 ሎጥ አመነታ፤ ያህዌ ምሕረት ስላደረገላቸው ሰዎቹ የእርሱ፣ የሚስቱንና የሁለት ሴት ልጆቹን እጅ ይዘው ከከተማዋ አወጣቸው። 17 ከከተማው ካወጧቸው በኋላ ከሰዎቹ አንዱ፣ "ሕይወታችሁን ለማዳን ሩጡ! ወደ ኋላችሁ አትመልከቱ፤ ወይም ረባዳው ስፍራ ላይ አትቆዩ። ወደ ተራሮች ሽሹ፤ አለበለዚያ ትጠፋላችሁ።" 18 ሎጥም እንዲህ አላቸው፤ "ጌቶቼ ሆይ፣ 19 እኔ ባሪያችሁ በፊታችሁ ሞገስ አግኝቻለሁ፤ ሕይወቴን ለማዳን ታላቅ ርኅራኄ አድርጋችሁልኛል፤ እኔ እንደ ሆንኩ ወደ ተራሮቹ ሸሽቼ ማምለጥ ስለማልችል የሚወርደው መዓት ደርሶ ያጠፋኛል። 20 ወደዚያ ሸሽቶ ለማምለጥ ቅርብ ቦታ ያለች ትንሽ ከተማ አለች ሸሽቼ ወደዚያ ብሄድ ሕይወቴን ማዳን እችላለሁ።" 21 እርሱም፣ "ይሁን እሺ፤ ልመናህን ተቀብብያለሁ፤ ያክካትንም ከተማ አላጠፋትም። 22 አንተ እዚያ እስክትደርስ ምንም ማድረግ ስለማልችል በል ቶሎ ፍጠንና ወደዚያ ሽሽ" አለው። ስለዚህ ያቺ ከተማ ዞዓር ተባለች። 23 ሎጥ ዞዓር ሲደርስ ፀሓይ በምድሩ ወጥታ ነበር። 24 ከዚያ ያህዌ ሰዶምና ጎሞራ ላይ ድኝና እሳት አዘነበ። 25 እነዚያን ከተሞችና ረባዳ ቦታዎቹን፣ የከተሞቹ ነዋሪዎችንና እዚይ ኣያሉ ለምለም ነገሮችን ሁሉ አጠፋ። 26 ከኋላው የነበረችው የሎጥሚስት ግን ወደ ኋላዋ ስለ ተመለከተች የጨው ዐምድ ሆና ቀረች። 27 አብርሃም ጠዋት ማለዳ ተነሥቶ ያህዌ ፊት ቆሞ ወደ ነበረበት ቦታ ሄደ። 28 ቁልቁል ሰዶምና ጎሞራን፣ እንዲሁም በረባዳው ስፍራ የነበረውን ምድር ተመለከተ። ከምድጃ የሚወጣ የመሰለ ጢስ ከምድሩ እየወጣ ነበር። 29 እግዚአብሔር በረባዳው ቦታ የነበሩ ከተሞችን ባጠፋ ጊዜ አብርሃምን አሰበው። ሎጥ የነበረበትን ከተሞች ቢያጠፋም፣ እርሱ ግን ከጥፋት መሐል አወጣው። 30 ሎጥ ግን በዞዓር መኖር ስለ ፈራ ከሁለት ሴቶች ልጆቹ ጋር ተራሮቹ ላይ ለመኖር ከዞዓር ወደ ላይ ወጣ። ስለዚህ እርሱና ሁለት ሴቶች ልጆቹ ዋሻ ውስጥኖሩ። 31 ታላቋ ልጅ ታናሿን እንዲህ አለቻት፣ "አባታችን አርጅቷል፤ በምድር ሁሉ እንደሚኖሩ ሰዎች ወግ ከእኛ ጋር የሚተኛ ወንድ በአካባቢያችን የለም። 32 ስለዚህ አባታችንን የወይን ጠጅ እናጠጣውና ከእርሱ ጋር እንተኛ፤ የትውልድ ሐረጋችን እንዳይቋረጥ ከአባታችን ዘር እናትርፍ።" 33 ስለዚህ በዚያ ምሽት አባታቸውን የወይን ጠጅ አጠጡት። ታላቂቱ ልጅ ሄዳ ክአባቷ ጋር ተኛች፤ እርሷ ስትተኛም ሆነ ስትነሣ አላወቅም። 34 በሚቀጥለው ቀን ታላቂቱ ታናሺቱን እንዲህ አለቻት፤ "ትናንት ሌሊት እኔ ከእባቴ ጋር ተኛሁ። ዛሬም እንደ ገና የወይን ጠጅ እናጠጣው፣ ከዚያ አንቺ ሄደሽ ከእርሱ ጋር ትተኛለሽ፣ የአባታችንንም ዘር እናተርፋለን።" 35 ስለዚህ በዚያም ምሽት አባታቸውን ወይን ጠጅ አጠጡት፤ ታናሺቱ ልጅ ሄዳ ከእርሱ ጋር ተኛች፤ እርሷ ስትተኛም ሆነ ስትነሣ አላወቀም። 36 ሁለቱ የሎጥ ልጆች ክአባታቸው አረገዙ። 37 ታላቂቱ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ስሙንም ሞዓብ አለችው። እርሱም ዛሬ ያሉት ሞዓባውያን አባት ሆነ። 38 ታናሺቱም እንዲሁ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ስሙንም ቤንአሚ አለችው። እርሱም ዛሬ ያሉት አሞናውያን አባት ሆነ።



Chapter 20

1 አብርሃም ከዚያ ተነሥቶ ወደ ኔጌብ አካብቢ ሄደ፤ በቃዴስና በሱር መካከልም መኖር ጀመረ። ለጥቂት ጊዜ በጌራራ ተቀመጠ። 2 አብርሃም ሚስቱ ሥራራን፣ "እኅቴ ናት" ይል ነበር፤ ስለዚህ ይጌራራ ንጉሥ አቢሜሌክ ሰዎች ልኮ ሣራን ወሰዳት። 3 እግዚአብሔር ግን በሕልም ወደ እቢሜሌክ መጥቶ፣ "እነሆ በወሰድካት ሴት ምክንያት አንተ ምውት ነህ፤ ምክንያቱም እርሷ ባለ ባል ናት" አለው። 4 አቢሜሌክ ገና አልሰረሰባትም ነበርና እንዲህ አለ፤ "ጌታ ሆይ፣ በደል ያልተገኘበትን ሕዝብ ልታጠፋ ነውን? 5 'እኅቴ ናት' ያለኝ እርሱ ራሱ አይደለምን? እርሷም ብትሆን 'ወንድሜ ነው' ብላኛለች። እኔ እንዲህ ያደረግሁት በቅን ልቦናና በንጹሕ እጅ ነው።" 6 በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር በሕልም እንዲህ አለው፤ "አዎን፣ ይህን ያደረግኸው በልብ ቅንነት እንደ ነበር እኔም አውቃለሁ፤ እኔ ላይ ኀጢአት እንዳትፈጽም የጠበቅሁህና እንዳትነካትም ያደረግሁት በዚህ ምክንያት ነው፤ 7 ስለዚህ የሰውየውን ሚስት መልስለት፤ እርሱ ነቢይ ስለ ሆነ ይጸልይልሃል አንትም ትድናለህ። እርሷን ካልመለስህ፣ እንተና የአንተ የሆነው ሁሉ በእርግጥ እንደምትጠፉ ዐውቃለሁ።" 8 አቤሜሊክ ጧት በማለዳ ተነሥቶ ሹማምንቶቹን ሁሉ ጠራ። የሆነውን ሁሉ ሲነግራቸው በጣም ፈሩ። 9 ከዚያም አቤሜሌ አብርሃምን አስጠርቶ፣ "ለመሆኑ፣ ምን እያደረግህብን ነው? በእኔና በግዛቴ ላይ እንዲህ ያለውን ትልቅ መዘዝ ያመጣህብኝ ምን ብበድልህ ነው? መደረግ ያልነበረትን አድርገህብኛል" አለው። 10 በመቀጠልም፣ አብርሃምን፣ "እንዲህ እንድታደርግ ያነሣሣህ ምንድን ነው?" ሲል ጠየቀው። 11 አብርሃምም፣ "በዚህ ቦታ እግዚአብሔርን መፍራት የለም፤ ለሚስቴ ሲሉ ይገድሉኛል በማለት ስላሰብሁ ነው። 12 በዚህ ላይ ደግሞ ከእናቴ ባትወለድም የአባቴ ልጅ እኅቴ ናት፤ በኋላም ሚስቴ ሆነች። 13 የአባቴን ቤት ትቼ በየአገሩ እንድዞር እግዚአብሔር ሲያዝዘኝ፣ "ለእኔ ለባልሽ ያለሽን ታማኝነት በዚህ አሳዪኝ፤ በምንሄድበት ቦታ ሁሉ 'ወንድሜ ነው' በዪ አልኳት።" 14 ከዚያ አቤሜሊክ በጎችና በሬዎች፣ ወንዶችና ሴቶች ባሪያዎች ለአብርሃም ሰጠው። ሚስቱ ሣራንም ለአብርሃም መለሰለት። 15 አቤሜሌክ እንዲህ አለ፤ "አገሬ አገርህ ነው፤ ደስ በሚያሰኝህ ቦታ ተቀመጥ።" 16 ሣራንም፣ "ለወንድምሽ አንድ ሺህ ጥሬ ብር እሰጠዋለሁ። ይህም፣ በአንቺ ላይ ለተፈጸመው በደል ካሣ እንዲሆንና አብረውሽ ያሉ ሁሉ አንቺ ንጹሕ ሴት መሆንሽን እንዲያውቁ ነው።" 17 ከዚያም አብርሃም ለአቤሜሌክ ጸለየ፤ እግዚአብሔርም አቤሜሌክን፣ ሚስቱንና ሴት አገልጋዮቹን ፈወሳቸው፤ ልጅ ለመውለድም በቁ። 18 ከአብርሃም ሚስት ከሣራ የተነሣ በአቢሜሌክ ቤት የሚገኙ ሴቶችን ሁሉ ያህዌ ማኅፀናቸውን ዘግቶ ነበር።



Chapter 21

1 ለአብርሃም በሰጠው የተስፋ ቃል መሰረት እግዚአብሔር ሳራን አሰባት፤ እንደገባላት የተስፋ ቃልም አደረገ ፤ 2 ስለዚህም ሳራ አርግዛ በእርጅናው ጊዜ ለአብርሃም ወንድ ልጅ ወለደችለት፤ ልጁም የተወለደው «በዚህ ጊዜ ይወለዳል» ብሎ እግዚአብሔር በተናገረበት ጊዜ ነው። 3 አብርሃም ሚስቱ ሳራ የወለደችለትን ልጅ «ይስሐቅ» ብሎ ስም አወጣለት። 4 ይስሐቅ ከተወለደ ከስምንት ቀን በኋላ እግዚአብሔር ባዘዘው መሰረት አብርሃም ገረዘው። 5 ልጁ ይስሐቅ በተወለደለት ጊዜ አብርሃም መቶ ዓመት ሆኖት ነበር። 6 ሳራም «እግዚአብሔር ሳቅ አደረገልኝ ስለዚህ ይህንን ነገር የሚሰማ ሁሉ ከእኔ ጋር ይስቃል»አለች። 7 ቀጥላም «ሳራ ለአብርሃም ልጆችን ወልዳ ታጠባለች» ብሎ የሚናገር ከቶ ማን ነበር አሁን ግን እነሆ በእርጅናው ዘመን ወንድ ልጅ ወለድሁለት» አለች። 8 ልጇም አድጎ ጡት መጥባት ተወ፤ ጡት ባስጣሉበትም ቀን አብርሃም ታላቅ ግብዣ አደረገ። 9 ግብጻዊትዋ አጋር ለአብርሃም የወለደችለት እስማኤል ከዕለታት አንድ ቀን በሳራ ልጅ በይስሐቅ ላይ ሲያሾፍበት ሳራ አየች። 10 ስለዚህ ሳራ አብርሃምን«ይህችን አገልጋይ ከነ ልጅዋ ወዲያ አባርልኝ የዚህች አገልጋይ ልጅ ከልጄ ከይስሐቅ ጋር አብሮ መውረስ አይገባውም» አለችው። 11 እስማኤልም ልጁ ስለሆነ ይህ ጉዳይ አብርሃምን በብርቱ አስጨነቀው 12 እግዚአብሔር ግን አብርሃምን «ስለ ልጁና ስለ አገልጋይቱ ስለ አጋር አትጨነቅ። ዘር የሚወጣልህ በይስሃቅ በኩል ስለሆን እርሳ የምትልህን ሁሉ አድርግ። 13 የአገልጋይቱም ልጅ የአንተ ዘርያ ስልሆን ታላቅ ሕዝብ አደርገዋለሁ» አለው 14 አብርሃም በማለዳ ተነሳ ጥቂት ምግብ ውሃም በአቁማዳ ለአጋር በትከሻዋ አደረገላት። ልጁንም በጀርባዋ አሳዝሎ ከቤት አስወጣት፤ እርስዋም በቤርሳቤህ በረሃ ትንከራተት ጀመር። 15 በአቁማዳ የነበረው ውሃ ባለቀ ጊዜ ልጁን በቁጥቋጦ ስር አስቀምችጠችው። 16 እርስዋም «ልጄ ሲሞት ማየት አልፈልግም» በማለት ጥቂት ከልጅዋ ርቃ ተቀመጠች፤ እዚያም ሆና ድምጻን ከፍ አድርጋ ታለቅስ ጀመር። 17 እግዚአብሔሬም ልሉ ምርር ብሎ ሲያለቅስ ሰማ የእግዚአብሔርም መልአክ ከሰማይ አጋርን «አጋር ሆይ የምትጨነቂበት ነገር ምንድር ነው? እግዚአብሔር የልጂን ለቅሶ ሰምቶአልና አትፍሪ። 18 ተነሺ ሂንና ልጁን አንስተስ አባብይው፤ የእርሱንም ዘር አበዛለሁ ታላቅ ሕዝብም አደርገዋለሁ። 19 በዚህም ጊዜ እግዚአብሔር ዓይኖችዋን ከፈተላትና አንድ የውኃ ጉድጋድ አየች፤ ሄዳም በአቁማዳ ውሃ ሞላች ለልጅዋም አጠጣችው። 20 ልጁ እያደገ በሚሄድበት ጊዜ ሁሉ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበር። 21 በፋራንም በረሓ ኖረ፤ ቀስት በመወርወርም የታወቀ አዳኝ ሆነ። እናቱም ከአንዲት ግብጻዊት ጋር አጋባችው። 22 በዚያን ጊዜ አቤሜሌክ ከሰራዊቱ አለቃ ከፊኮል ጋር ሄደና አብርሃምን «በምታደርገው ሁሉ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነው፤ 23 እኔንም ሆነ ልጆቼን ወይም ዝርያዎቼን እንዳትዋሸኝ አሁን በእግዚአብሔር ስም ማልልኝ። እኔ ለአንተ ታማኝነትን አሳይቻለሁ፤ አንተም ለእኔና ለዚህች ለምትኖርባትአገር ታማኝንትን እንደምታሳይ ማልልኝ» አለው። 24 አብርሃምም «እሺ እምላለሁ» አለ። 25 አብርሃም የአቢሜሌክ አገልጋዮች ስለ ወሰዱበት የውሃ ጉድጋድ ለአቤሜሌክ አቤቱታ አቀረበ፤ 26 አቤሜሌክም «ይህን ያደረገ ማን እንደሆን አላውቅም። አንተም አልነገርኸኝም ይህንን ነገር ገና ዛሬ መስማቴ ነው» አለው። 27 ከዚህ በኋላ አብርሃም ብዙ በጎችና ከብቶች አምጥቶ ለአቢሜሌክ ሰጠው፤ በዚያን ቀን ሁለቱም የስምምነት መሀላ አደረጉ። 28 በዚያን ጊዜ አብርሃም ሰባት እንስት የበግ ጠቦቶችን ከመንጋው ለየ፤ 29 አቤሜሌክም «እንዚህን ሰባት ጠቦቶች ለይተህ ያቆምሃቸው ለምንድር ነው?» አለው። 30 አብርሃምም «እነዚህን ሰባት እንስት ጠቦቶች ተቀበለኝ እነርሱን ከተቀበልከኝ ይህን ጉድጋድ የቆፈርሁ እኔ መሆኔን ምስክር እንዲሆን ነው» አለው፤ 31 ሁለቱ ተማምለው የተስማሙበት ስፍራ በመሆኑ የዚያ ቦታ ስም ቤርሳቤህ ተባል፤ 32 ይህን ስምምንት በቤርሳቤህ ተስማምተው ካደረጉ በኋላ አቤሜሌክና የሰራዊቱ አለቃ ፊኮል ወደ ፍልስጥኤም ምድር ተመለሱ 33 ከዚህ ብኃላ አብርሃም በቤርሳቤህ የታማሪስክ ዛፍ ተከልና የዘላለም አምላክ ለሆነው ሰገደ፤ 34 አብርሃም በፍልስጥኤም ምድር በእንግድነት ለረዥም ጊዜ ኖረ።



Chapter 22

1 ሁሉ ነገር በኋላ እግዚአብሔር አብርሃምን ፈተነው፤ እግዚአብሔርም «አብርሃም»ብሎ ጠራው፤ «እነሆ አለሁኝ» ብሎ መለሰ። 2 እግዚአብሔርም «የምትወደውን አንድ ልጅህን ወደ ሞሪያ ምድር ሂድ። እዚያ በማሳይህ አንድ ኮረብታ ላይ እርሱን የሚቃጠል መስዋዕት አድርገህ አቅርብልኝ» አለው፤ 3 አብርሃም በማለዳ ተነስቶ ለመስዋዕት የሚሆን እንጨት ቆረጠና በአህያው ላይ ጫነው፤ከእርሱ ጋር ልጁን ይስሐቅን ና ሁለት ወጣት ሰዎችን ይዞ እግዚአብሔር ወደ ነገረው ቦታ ለመሄድ ጉዞ ጀመረ። 4 በሦስተኛው ቀን አብርሃም ቀና ብሎ ሲመለከት ቦታውን በሩቅ አየ። 5 ከዚህ በኃላ አብርሃም የርሱን ወጣቶች «እናንተ ከአህያው ጋር በዚህ ቆዩ እኔና ልጄ ወደዚያ ሄደን ከሰገድን በኃላ እንመለሳለን፤ 6 አብርሃምም የሚቃጠለውን መስዋዕቱን ማቃጠያ እንጨት አንስቶ ለልጁ ለይስአቅ አሸከመው፤ እርሱ ግን ቢላዋውንና እሳቱን ያዘ ሁለቱም አብረው ሄዱ። 7 ይስሐቅ አብርሃምን «አባባ» አለው፤ እርሱም «እነሆ አለሁ ልጄ» አለው፤ ይስሐቅም «እነሆ እሳትና እንጨት ይዘናል ታዲያ ለመስዋዕት የሚሆነው በግ የት አለ?» በማለት አብርሃምን ጠየቀው። 8 አብርሃምም «ልጄ ሆይ ለመስዋዕት የሚሆነውን በግ እግዚአብሔር እራሱ ያዘጋጃል» አለው። ሁለቱም አብረው መንገዳቸውን ቀጠሉ። 9 እግዚአብሔር ነገረው ቦታ በደረሱ ጊዜ አብርሃም መሰዊያ ሰርቶ እንጨቱን ረበረበው፤ ልጁን ይስሐቅንም አስሮ ከእንጨቱ በላይ በመሰዊያው ላይ አጋደመው። 10 ልጁን ለማረድ ቢላዋ አንስቶ እጁን ዘረጋ። 11 ነገር ግን የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ «አብርሃም! አብርሃም!» ብሎ ጠራው። እርሱም «እነሆኝ አለሁኝ» አለ። 12 እርሱም «በልጁ ላይ እጅህን አትጫንበት፣ ምንም ዓይነት ጉዳትም አታድርስበት፣ እነሆ እግዚአብሔርን የምትፈራ መሆንህን ተረድቻለሁ፤ አንድ ልጅህን እንኳ ለእኔ ከመስጠት አልተቆጠብህም» አለው። 13 አብርሃም ዙሪያውን በተመለከት ጊዜ ከበስተጀርባው ቀንዶቹ በቁጥቋጥ ዛፍ የተያዙ አንድ በግ አየ፤ አብርሃምም ሄዶ በጉን አመጣና በልጁ ፋንታ የሚቃጠል መስዋዕት አድርጎ አቀረበው። 14 አብርሃምም ያን ቦታ «እግዚአብሔር ያዘጋጃል» ብሎ ጠራው። ዛሬም ቢሆን ሠዎች «እግዚአብሔር በተራራው ላይ ያዘጋጃል» ይላሉ። 15 የእግዚአብሔር መልአክ ለሁለተኛ ጊዜ አብርሃምን ከሰማይ ጠራውና፤ 16 እንዲህ አለው፤ «እግዚአብሔር ብዙ በረከት እንድምሰጥህ በራሴ ስም እምላለሁ» ይላል፤ ይህን ስላደረግህና አንድ ልጅህንም ለእኔ ለመስጠት ስላልተቆጠብህ፤ 17 እኔም ዘርህን እንደ ሰማይ ከዋክብትና እንደ ባህር ዳር አሸዋ አበዛዋለሁ፤ ዝርያዎችህም ጠላቶቻቸውን ድል ነስተው፤ ከተሞቻቸውን ይይዛሉ። 18 ትዕዛዜን ስለ ፈጸምህ የዓለም ህዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ»፤ 19 ከዚህ በኋላ አብርሃም ወደ ወጣቶችሁ ተመለሰና በአንድነት ሆነው ወደ ቤርሳቤህ ሄዱ፤ አብርሃምም በቤርሳቤህ ተቀመጠ። 20 ከዚህ ሁሉ በኋላ እንዲህ ተብሎ ለአብርሃም ተነገረው «ሚልካ ልጆችን ለወንድምህ ለናኮር ወልዳለች፤ 21 እነርሱም የመጀመሪያው ልጅ ዑፅ ወንድሙም ቡዝ የአራም አባት ቀሙኤል፤ 22 ኬሰድ፣ ሐዞ፣ ፊልዳሽ፤ ይድላፍና በቱኤል ናቸው። 23 በቱኤል ርብቃን ወለደ። ሚልካ እነዚህን ስምንት ልጆች ለአብርሃም ወንድም ለንኮር ወለደችለት፤ 24 ረኡማ የተባለች የናኮር ቁባት ደግሞ ጤባሕን፣ ገሐምን፣ ተሐሽና ማዕካን ወለደችለት።



Chapter 23

1 ሣራ መቶ ሃያ ሰባት ዓመት ኖረች። እነዚህን ዓመታት ነበር ሳራ የኖረችው። 2 በከነዓን ምድር ባለችው ቂርያት አርባ ተብላ በምትጠራው በኬብሮን ከተማ ሞተች፤ አብርሃም በሣራ ሞት ምክንያት እጅግ ሃዘነ አለቀሰም። 3 ከዚያም አብርሃም ከተቀመጠበት ከሚስቱ ሬሳ አጠገብ ተነሳ፣ ኬጢያውያንን እንዲህ አላቸው፤ 4 «እኔ በመካከላችሁ በእንግድነት የምኖር ነኝ። እባካችሁ የመቃብር ቦታ ስጡኝ፤ የሚስቴንም ሬሳ ልቅበርበት።» 5 የኬጢ ልጆችም ለአብርሃም እንዲህ ሲሉ መለሱለት፤ 6 «ጌታ ሆይ ስማን፣ አንተ በእኛ መካከል ከእግዚአብሔር አለቃ ነህ። ከመቃብር ቦታችን በመረጥከው ስፍራ ሬሳህን መቅበር ትችላለህ፣ ማናችንም ብንሆን የሞተብህን ሰው እንዳትቀብርበት የምቃብር ቦታችንን አንከለክልህም።» 7 አብርሃም ተነሣ በኬጢያውያን ልጆች ፊት እጅ ነስቶ እንዲህ አለ። 8 የሚስቴን አስከሬን እዚህ እንድቀብር ከፈቀዳችሁልኝ የጾሐር ልጅ ዔፍሮምን ስለ እኔ ሆናችሁ ልምኑልኝ፤ 9 በእርሻው ዳር ያለችውን መክፈል የተባለችውን ዋሻውን እንዲሸጥልኝ ጠይቁልኝ፣ ይህ ስፍራ የመቃብር ቦታ እንዲሆንልኝ በእናንት ፊት ሙሉ ዋጋ ከፍዬ እንድገዛው አድርጉልኝ።» 10 ኤፍሮንም በኬጢ ልጆች መካከል ተቀምጦ ነበር፤ የኬጢም ሰው ኤፍሮንም የኪጥ ልጆችና ወደ ከተማ የሚገቡ ሲስሙ ለአብርሃም እንዲህ ሲል መለሰለት፤ 11 «አይደለም ጌታዬ፣ ስማኝ። እርሻውን፣ በርሱም ዳር ያለውን ዋሻ፤ በወገኔ ልጆች ፊት ሰጥቼአለሁ። ሬሳህን ቅበር።» 12 አብርሃምም በአገሩ ሰዎች ፊት ሰገደ። 13 የአገሩ ሰዎችም እየሰሙ ለኤፍሮን እንዲህ ሲል ተናገረ፤ «እባክህ ፈቃደኛ ብትሆን አድምጠኝ፤ የእርሻውን ዋጋ እሰጥሃለሁ። አንተም ከእኔ ዘንድ ውሰድ፤ ሬሳዬንም በዚያ እቀብራለሁ 14 ኤፍሮንም ለአብርሃም እንዲህ ሲል መለሰለት፤ 15 «ጌታዬ ሆይ እኔን ስማኝ፤ የመሬቱ ዋጋ እራት መቶ ሰቅል ቢሆን ነው፤ ታዲያ ይሄ በእኔና በአንተ መካከል ምንድር ነው? ሬሳህንም ቅበር» 16 አብርሃምም የኤፍሮንን ነገር ሰማ፤ አብርሃምም በኬት ልጆች ፊት የነገረውን አራት መቶ ሰቅል መዝኖ ለኤፍሮን ሰጠው፤ ብሩንም በወቅቱ የንግድ መለኪያ መሰረት መዘነለት። 17 በዚህም ሁኔታ በመምሬ አጠገብ በመክፈላ ያለውን የኤፍሮንን እርሻ ቦታ ከነዋሻው በከልሉ ካሉት ዛፎች ሁሉ ጭምር ለአብርሃም በርስትነት ተላለፈ፤ 18 እርሻው በእርሱ ያለውን ዋሻው በእርሻውም ውስጥ በዙሪያውም ያለው እንጨት ሁሉ በኬጢ ልጆችና በከተማይቱ በር በሚገቡ ሁሉ ፊት ለአብርሃም ርስቱ ሆነ። 19 ከዚያም በኋላ ኬብሮን በምትባል በምምሬ ፊት በከነአን ፊት ባለው እርሻ ባለ ድርብ ክፍሌ በሆነው ዋሻ ውስጥ ሚስቱን ሳራን ቀበረ። 20 እርሻውና በርሱ ያለው ዋሻው በኪጥ ልጆች ዘንድ ለአብርሃም የመቃብር ርስት ሆኖ ጸና።



Chapter 24

1 በዚህ ጊዜ አብርሃም ሸመገለ፤ ዕድሜውም ገፋ፤ እግዚአብሔርም አብርሃምን በሁሉ ነገር ባረከው። 2 አብርሃምም የንብረቱ ሁሉ ኀላፊ የቤቱ ሁሉ አዛዥ የሆነውን አገልጋይ እንዲህ አለው፤ እጅህን ከጭኔ በታች አድርግ 3 እኔም በመካከላቸው ከምኖረው ከከነዓናዊያን ለልጄ ሚስት እንዳታጭለት በሰማይና በምድር አምላክ እግዚአብሔር አስምልሃለሁ። 4 ነገር ግን ወደ ገዛ ሀገሬ እና ወደ ወገኖቼ ሄደህ ለልጄ ለይስሐቅ ሚስትን ታጭለታለህ። 5 አገልጋዩም «ምናልባት የምመርጥለት እጮኛ ከእንይ ጋሬ ወደዚህ አገር ለመምጣት እምቢ ብትልስ? ልጅህን ቀድሞ አንተ ወደ ነበርክበት አገር እንዲመለስ ላድርገው?» ብሎ ጠየቀ። 6 አብርሃም ግን እንዲህ አለው፤ «በምንም ዓይነት ምክንያት ቢሆን ልጄን ወደዚያ አገር መልሰህ እንዳትወስድ ተጠንቀቅ፤ 7 የሰማይ አምክክ እግዚአብሔር ከአባቴ ቤትና ከትውልድ አገሬ አውጥቶ አምጥቶኛል፤ ይህንንም ምድር ለዝርያዎቼ እንደሚሰጥ በመሃላ ቃል ገብቶልኛል፤ ከዚያ ለልጄ ሚስት ማግኘት እንድትችል እግዚአብሔር መልአኩን በፊትህ ይልካል። 8 ልጅትዋ ከአንተ ጋር ለመምጣት ፈቃደኛ ባትሆንከዚህ መሓላ ነፃ ትሆናለህ፤ ልጄን ግን በምንም ዓይነት ሁኔታ ወደዚያ አትመልሰው።» 9 ከዚህ በኋላ አገልጋዩ እጁን በጌታው በአብርሃም ጉልበት ላይ አድርጎ አብርሃም ያዘዘውን ሁሉ እንደሚፈፅም በመሐላ ቃል ገባ። 10 የአብርሃም ንብረት ኀላፊ የነበረው መጋቢ ከጌታው ቤት ምርጥ የሆኑ የስጦታ ዕቃዎችን በዕሥር ግመሎች ጭኖ በሰሜን መስጴጦምያ ናኮር ወደሚኖርበት ከተማ ሄደ። 11 እዚያ በደረሰ ጊዜ ከከተማው ውጭ ባለ የውሃ ጉድጓድ አጠገብ ግመሎቹ ተንበርክከው እንዲያርፉ አደረገ፤ ሰዓቱም ሊመሽ ተቃርቦ፣ ሴቶች ውሃ ለመቅዳት የሚወጡበትን ጊዜ ነበር፤ 12 አገልጋዩ እንዲህ ብሎ ጸለየ፣ "የጌታዬ የአብርሃም አምላክ እግዚአብሔር ሆይ! ዛሬ የእኔን አሳብ በመፈፀም ለጌታዬ ለአብርሃም ዘላለምዊ ፍቅርህን ግለጥ። 13 እነሆ፣ እኔ በዚህ የውሃ ጉድጓድ አጠገብ ቆሜአለሁ፤ የከተማይቱም ልጃገረዶች ውሃ ሊቀዱ ወደዚህ ይመጣሉ፤ 14 ከእነሱም አንድዋ ልጃገረድ 'እንስራሽን ዘንበል አድርገሽ ውሃ አጠጪኝ' እላታለሁ፤ 'አንተም ጠጣ፤ ግመሎችህም እንዲጠጡ ውጃ ቀድቼ አመጣለሁ' ካለችኝ ለአገልጋይህ ለይስሐቅ ፍቅርህን እንዳሳየኸው ዐውቃለሁ።" 15 ገና ጸሎቱን ሳፅቸርስ ርብቃ እንስራ ተሸክማ መጣች፤ የዚህችም ልጅ አባት ባቱኤል ይባል ነበር፤ እርሱም የአብርሃም ወንድም ናኮር ከሚስቱ ከሚልካ የወለደው ነው። 16 ርብቃ ገና ወንድ ያልደረሰባት በጣም ቆንጆ ልጃገረድ ነበረች፤ እርስዋ ወደ ውሃው ጉድጓድ ወርዳ በእንስራዋ ውሃ ከቀዳች በኋላ ተመለሰች። 17 አገልጋዩም ወደ እርስዋ ሮጦ ሄዳና "እባክሽ ከእንስራሽ ከእንስራሽ ጥቂት ውሃ አጠጪኝ"አላት። 18 እርስዋም "እሺ ጌታዬ ጠጣ" አለችና እንስራዋን ከትከሻዋ አውርዳ ዘንበል አድርጋ ያዘችለት። 19 ጠጥቶም ከረካ በኋላ "ለግመሎችህም ውሃ እቀዳላቸዋለሁ፤ እስኪበቃቸውም ድረስ ይጠጡ" አለችው። 20 ወዲያውኑ፤ በእንስራዋ የያዘችውን ውሃ ግመሎቹ በሚጠጡበት ገዳን ላይ ገልብጣ ግመሎቹ ሁሉ ጠጥተው እስከሚረኩ ድረስ እየተጣደፈች ከጉድጓድ ውሃ መቅዳት ቀጠለች። 21 ሰውየውም እግዚአብሔር የሄደበትን ተልእኮ አቃንቶለት እንደሆን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ሁሉ ዝም ብሎ ይመለከት ነበር። 22 ግመሎቹ ጠጥተው በኋላ ሰውየው አምስት ግራም ያህል የሚመዝን የወርቅ ጎታቻ አውጥቶ በጆሮዋ ላይ አደረገላት፤ መቶ ዐሥር ግራም ያህል የሚመዝን ሁለት የወርቅ አምባሮችንም አውጥቶ በእጆችዋ ላይ አደረገላትና፤ 23 "የማን ልጅ ነሽ? እስቲ እባክሽ ንገሪኝ፤ ለእኔና አብረውኝ ቤት ይገኛልን?" ብሎ ጠየቃት። 24 እርስዋም "የባቱኤል ልጅ ነኝ፤ የባቱኤል አባት ናኮር፣ እናቱም ሚልካ ይባላሉ፤ 25 በቤታችን ብዙ ገለባና ድርቆሽ አለ፤ ለእናንተም ማደሪያ ቦታ ይገኛል" አለችው። 26 ሰውየምውም በመንበርከክ ለእግዚአብሔር ሰግዶ፣ 27 "ለጌታዬ የገባውን ቃል ኪዳንና ዘላለማዊ ፍቅሩን የጠበቀ የጌታዬ የአብርሃም አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን፤ በቀጥታ መርቶ ወደ ጌታዬ ወንድሞች ቤት ያመጣኝ እርሱ ነው" አለ። 28 ልጅትዋ ወደ ቤት ሮጣ ሄደችና የሆነውን ሁሉ ለእናትዋና ለእርስዋ ጋር ላሉት ሁሉ ነገረቻቸው። 29 ርብቃ ላባ የተባለ ወንድም ነበራት፤ እርሱ የአብርሃም አገልጋይ ወዳለበት ውሃ ጉድጓድ እየሮጠ ሄደ። 30 ላባ ወደ ሰውየው የሄደው እኅቱ በጆሮዋ ላይ ያደረገችውን ጉትቻና በእጆችዋ ላይ ያደረገቻቸውን አንባሮች ስላየና ርብቃ ሰውየው ጉድጓድ አጠገብ ከግመሎቹ ጋር ቆሞ አገኘው። 31 ስለዚህ ላባ "አንተ እግዚአብሔር የባረከህ ሰው! ና ወደ ቤት እንሂድ፤ በውጭ የቆምኸው ለምንድን ነው? በቤታችን ለአንተ ማደሪያ የተዘጋጀ ቦታ አለ" አለው። 32 ከዚህ በኋላ ሰውየው ወደ ቤት ሄደ፤ ላባም በግመሎቹ ላይ የነበረውን ጭነት አረግፎ ገለባና ድርቆሽ አቀረበላቸው፤ ቀጥሎም የአብርሃም አገልጋይና አብረውት የነበሩት ሰዎች እግራቸውን የሚታጠቡበትን አመጣላቸው። 33 ገበታ በቀረበው ጊዜ ጊዜ ሰውየው "የተላክሁበትን ጎዳይ ከመናገሬ በፊት እህል አልቀምስም" አለ። ላባም "ይሁን ተናገር" አለው። 34 እርሱም "እኔ የአብርሃም አገልጋይ ነን፤ 35 እግዚአብሔር ጌታዬ እጅግ ባርኮል፤ ባለጸጋም አድርጎታል፤ ብዙ የበግ፣ የፍየልና የከብት መንጋ፣ ብርና ወርቅ፣ ወንዶችና ሴቶች አገልጋዮች ግመሎችና አህዮች ሰጥቶታል። 36 የጌታዬ ሚስት ሣራ በእርጅናዋ ዘምን ወንድ ልጅ ወልዳለታለች፤ ጌታዬም ያለውን ሀብት ሁሉ ለዚሁ ልጅ አውርሶታል። 37 ጌታዬ አብርሃም 'እኔ በመካከላቸው ከምኖረው ከከነዓናዊያን ሴቶች ልጆች መካከል ለልጄ ሚስት እንዳላጭለት፤ 38 ነገር ግን ወደ አባቴ ቤተሰብና ወደ ዘመዶቼ ሄደህ ለልጄ ሚስት እጭለት' ሲል በመሐላ ቃል ኪዳን አስገብቶኛል።' 39 እኔም ጌታዬን 'ልጅቷ ከእኔ ጋር ለመምጣት ፈቃደኛ ባትሆንስ ምን ላድርግ?' ብዬ ጠየኩት። 40 እርሱም እንዲህ አለኝ 'ዘውትር የማገለግለው እግዚአብሔር መልአኩን ከአንተ ጋር ይልካል፤ ጉዞህም የተቃና እንዲሆን ያደርጋል፤ በዚህ ሁኔታ አንተም ከአባትቴ ቤተሰብና ከዘመዶቼ መካከል ለልጄ ሚስት ልታጭለት ትችላለህ፤ 41 ከመሐላህ ነፃ የምትሆነው ወደ ዘመዶቼ ሄደህ እነርሱ ልጅትዋን አንሰጥም ብለው የከለከሉህ እንደሆነ ብቻ ነው።' 42 "ከዚያም በኋላ ዛሬ ወደ ውሃው ጉድጓድ ስመጣ እንዲህ ብዬ ጸለይሁ 'የጌታዬ የአብርሃም አምላክ እግዚአብሔር ሆይ! እባክህ የመጣሁበት ጉዳይ እንዲቃና አድርግልኝ፣ 43 እነሆ በዚህ ውሃ ጉድጓድ አጠገብ ቆሜአለሁ፤ አንዲት ልጃገረድን ውሃ ልትቀዳ ስትመጣ፣ 'እባክሽ ከእንስራሽ ጥቂት ውሃ አጠጪኝ' ብዬ እጠይቃታለሁ፤ 44 እርስዋም 'እሺ ጠጣ፤ ለግመሎችህም እቀዳቸዋለሁ'የምትለኝ ብትሆን፣ ለጌታዬ ልጅ ሚስት እንድትሆን አንተ የመረጥሃት እርስዋ ትሁን። 45 የኅሊና ጸሎትን ገና ሳልጨርስ ርብቃ እንስራ ተሸክማ ብቅ አለች፤ ወደ ጉድጓዱም ሄዳ ውሃ ቀዳች፤ እኔም 'እባክሽ ጥቂት ውሃ አጠጪኝ አልኋት። 46 እርስዋም እንስራዋን በፍጥነት ከጀርባዋ አወረደችና ዘንበል አድርጋ 'እሺ ጠጣ፤ ግመሎችህንም አጠጣልሃለሁ' አለችኝ፤ ስለዚህ እኔም ጠጣሁ፤ ግመሎቼንም አጠጣችልኝ። 47 እኔም 'የማን ልጅ ነሽ?' ብዬ ጠየቅኋት። እርስዋም 'የባቱኤል ልጅ ነኝ፤ የባቱኤል አባት ናኮር እናቱም ሚልካ ይባላሉ' አለችኝ። ከዚህ በኋላ ጉትቻ በጆሮዋ ላይ፣ አንባሮቹንም በእጅዎችዋ ላይ አደረግሁላት፤ 48 ከዚህ በኋላ በጉልበቴ ተንበርክኬ ለእግዚአብሔር ሰገድሁ፤ የጌታዬን የአብርሃም አምላክ እግዚአብሔር አመሰገንሁ፤ ምክንያቱም ለጌታዬ ልጅ ሚስት የምትሆነዋን ሴት ወዳገኘሁበት ወደ ጌታዬ ወንድም ቤት በቀና መንገድ የመራኝ እርሱ ነው። 49 እንግዲህ የጌታዬን ዐደራ በእውነት ተቀብላችሁ እርሱን ደስ ለማሰኘት የምትፈቅዱ እንደሆነ ንገሩኝ፤ የማትፈቅዱም እንደሆነ ቁርጡን ነገሩኝ፤ እኔም እግዚአብሔር ወደሚመራኝ እሄዳለሁ።" 50 ላባና ባቱኤልም "ይህ ነገር ከእግዚአብሔር የመጣ ስለሆነ፣ መከልከል አልችልም፤ 51 ርብቃ ይችውልህ፤ እነሆ ይዘሃት ሂድ፤ እግዚአብሔር ራሱ እንደተናገረው ለጌታዬ ልጅ ሚስት ትሁን" አሉት። 52 የአብርሃም አገልጋይ ይህን በሰማ ጊዜ በጉልበቱ ተንበርክኮ ለእግዚአብሔር ሰገደ፤ 53 ከውርቅና ከብር የተሠሩ ጌጣጌጦችን፣ እንዲሁም ልብስ አውጥቶ ለርብቃ ሰጣት፤ ለወንድምዋና ለእናትዋም በጣም ውድ የሆኑ ስጦታዎችን አውጥቶ ሰጣቸው። 54 ከዚህ በኋላ የአብርሃም አገልጋይና አብረውት የነበሩ ሰዎች በልተው ጠጥተው እዚያው አደሩ፤ ጠዋት በተነሡ ጊዜ የአብርሃም አገልጋይ "እንግዲህ ወደ ጌታዬ እንድመለስ ፍቀዱልኝ" አለ። 55 ነገር ግን የርብቃ ወንድምና እናትዋ "ልጅትዋ ዐሥር ቀን ያህል ከእኛ ጋር ትቆይ፤ ከዚህ በኋላ ከአንተ ጋር ልትሄድ ትችላለች" አሉት። 56 እርሱ ግን "እባካችሁ አታቆዩኝ፤ እግዚአብሔር የመጣሁበትን ጉዳይ ስላቃናልኝ ቶሎ ብፄ ወደ ጌታዬ ልመለስ" አላቸው። 57 እነርሱም "እስቲ ልጅቷን እንጥራትና እርስዋ የምትለውን እንስማ" አሉ። 58 ስለዚህ ርብቃን ጠሩና "ከዚህ ሰው ጋር መሄድ ትፈልጊያለሽ?" ብለው ጠየቅዋት። እርስዋም "አዎ እሄዳለሁ"አለች። 59 ስለዚህ ርብቃ ሞግዚትዋን አስከትላ፣ ከአብርሃም አገልጋይና ከእርሱ ሰዎች ጋር እንድትሄድ ፈቀዱላት። 60 "አንቺ እኅታችን የብዙ ሺ ሕዝብ እናት ሁኚ፤ ዝርያዎችሽም የጠላቶችሽን ከተሞች ይውረሱ" ብለው ርብቃን መረቁአት። 61 ከዚህ በኋላ ርብቃ ከተከታዮችዋ ጋር ለመሄድ ተነሣች፤ በግመሎቹ ላይ ተቀምጠው ከአብርሃም አገልጋይ ጋር ለመሄድ ተዘጋጁ። በዚህ ዐይነት የአብርሃም አገልጋይ ርብቃን ይዞ ሄደ። 62 በዚህ ጊዜ ይስሐቅ "ብኤር ላሐይ ሮኤ ወይም የሚያየኝን ሕያው አምላክ"የተባለው ኩሬ ወዳለበት በረሓ መጥቶ በኔጌብ ተቀምጦ ነበር። 63 ከለዕታት አንድ ቀን ወደ ማታ ጊዜ እያሰላሰለ በመስክ ውስጥ ሲዘዋወር ሳለ ግመሎች ሲመጡ በሩቅ አየ። 64 ርብቃ ይስሐቅ ባየች ጊዜ ከግመሏ ወረደችና፣ 65 "ያ በመስክ ውስጥ ወደ እኛ የሚመጣው ሰው ማን ነው?" ስትል የአብርሃምን አገልጋይ ጠየቀችው። አገልጋዩም "እርሱ ጌታዬ ነው!" አላት። ስለዚህ በጥፍነት በሻሽ ፊትዋን ሸፈነች። 66 አገልጋዩም ያደረገውም ነግር ሁሉ ለይስሐቅ ነገረው። 67 ከዚህ በኋላ ይስሐቅ እናቱ ሣራ ትኖርበት ወደነበረው ድንኳን ርብቃን ይዞአት ገባ፤ ሚስትም ሆነችው፤ ይስሐቅ ርብቃን ወደዳት፤ በእናቱ ሞት ምክንያት ከደረሰበትም ሐዘን በዚህ ሁኔታ ተጽናና።



Chapter 25

1 አብርሃም ቀጡራ የምትባል ሌላ ሚስት አገባ፤ 2 እርስዋም ዚምራንን፣ ዮቅሻንን፣ መዳንን፣ ምድያምን፣ ዩሽባቅንና ሹሐን ወለደችለት። 3 ዮቅሻንም ሳባንና ደዳንን ወለደ፤ የዳደንም ዝርያዎች አሹራውያን፣ ሌጡሻውያንና ሌአማውያን ናቸው። 4 የምድያም ልጆች ዔፋ፣ ዔፈር፣ ሐኖክ፣ አቢዳዕና ኤልዳዓ ናቸው፤ እነዚሁ ሁሉ የቁጠራ ዝርያዎች ናቸው። 5 አብርሃም ያለው ሀብት ሁሉ ለይስሐቅ አወረሰው፤ 6 ከሌሎች ሴቶች ለተወለዱትም ልጆች ገና በሕይወት ሳለ ስጦታ ሰጣቸው፤ ከዚህ በኋላ እነዚህ ሌሎች ልጆች ከይስሐቅ ርቀው ወደ ምሥራቅ አገር እንዲሄዱ አደረጋቸው። 7 የአብርሃም ዕድሜ በአጠቃላይ መቶ ሰባ አምስት ዓመት ነበር፤ 8 በዚህም ዐይነት አብርሃም በቂ ዕድሜ አግኝቶ ካረጀ በኋላ ሞተ፤ 9 ልጆቹ ይሰሐቅና እስማኤል ማክጴላ በተባለ ዋሻ ቀበሩት፤ ይህም ዋሻ ከመምሬ በስተምሥራቅ በሒታዊ በጶሐር ልጅ በዔፍሮን እርሻ ውስጥ የሚገኘው ነው። 10 እነሱም አብርሃም ከሒታዊያን ላይ የገዛው የመቃብር ቦታ ነው፤ በዚህ ዐይነት አብርሃም ሚስቱ ሣራ በተቀበረችበት ዋሻ ተቀበረ። 11 አብርሃም ከሞተ በኋላ ልጁን ይስሐቅን እግዚአብሔር ባረከው፤ ይስሐቅ "ብኤርላሐይሮኢ ወይም የሚያየኝ ሕያው አምላክ" ተብሎ በመጠራት ኩሬ አጠገብ ይኖር ነበር። 12 የሣራ አገልጋይ ግብፃዊትዋ አጋር ለአብርሃም የወለደችለትን እስማኤል፤ 13 ከዚህ በታች በዕድሜአቸው ቅደም ተከተል ተራ የተዘረዘሩትን ልጆች ወለደ፤ እነርሱም፦ ነባዮት፣ ቄዳር፣ አድብኤል፣ ሚብሣም፣ 14 ሚሽማዕ፣ ዱማ፣ ማሣ፣ 15 ሐዳድ፣ ቴማ፣ ይጡር፣ ናፊሽና ቄድማ ናቸው። 16 እነዚህ የእስማኤል ልጆች ለአሥራ ሁለት ነገዶች ቅድመ አያቶች ነበሩ፤ ስማቸውም በኖሩባቸው ከተሞችና ስፍራዎች ሲጠራ ይኖራል። 17 እስማኤል መቶ ሠላሳ ሰባት ዓመት ሲሆነው ሞተ። 18 የእስማኤል ዝርያዎች ከግብፅ በስተምጅራቅ ወደ አሦር በምትወስደው መንገድ በሐዊላና በሹር መካከል ይኖሩ ነበር። የኖሩበትም ከሌሎቹ የአብርሃም ዝርያዎች ጋር በጥላቻ ተራርቀው ነበር። 19 የአብርሃም ልጅ ይስሐቅ ታሪክ ይህ ነው። አብርሃም ይስሐቅን ወለደ። 20 ይስሐቅ የባቱኤልን ልጅ ርብቃን ሲያገባ አርባ ዓመት ሆኖት ነበር፤ የርብቃ አባት ባቱኤልና ወንድምዋ ላባ በመስጴጦምያ የሞኖሩ ሶሪያውያን ነበሩ። 21 ርብቃ መኻን ስለ ነበረች ይስሐቅ ስለ እርስዋ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፤ እግዚአብሔርም ጸሎቱን ስለ ሰማ ርብቃ ፀነሰች፤ 22 የተፀነሱትም መንትያዎች ስለነበሩ እርስ በርሳቸው በማሕፀንዋ ውስጥ ይገፋ ነበር፤ እርስዋም "ይህን ዐይነት በገር ለምን ደረሰብኝ?" በማለት ወደ እግዚአብሔር ለመጸለይ ተነሣሣች። 23 እግዚአብሔርም ያሉት ሁለት ሕዝቦች ናቸው፤ እርስ በርሳቸው የማይስማሙ ሁለት ወገኖች ትወልጃለሽ፤ አንዱም ከሌላው የበረታ ይሆናል፤ ታላቁም ታናሹ አገልጋይ ይሆናል" አላት። 24 የመውለጃዋም ሰዓት በደረሰ ጊዜ ሁለት ወንዶች ልጆች ወለደ። 25 የመጀመሪያው ልጅ መልኩ ቀይ፣ ሰውነቱ ጠጉራም ነበር፤ ስለዚህ ዔሳው ተባለ። 26 ሁለተኛው ልጅ ሲወለድ የዔሳውን ተገረዝ ይዞ በመውጣቱ ያዕቆብ ተባለ፤ ልጆቹ በተወለዱ ጊዜ ይስሐቅ ስልሳ ዓመት ሆኖት ነበር። 27 ሁለቱም ልጆች አደጉ፤ ዔሳው በዱር መዋል የሚወደ ብልኅ አዳኝ ሆነ፤ ያዕቆብ ግን በቤት መዋል የሚወድ ጭምት ሰው ነበር። 28 ይስሐቅ ዔሳውን ይወድ ነበር። ምክንያቱም ዔሳው እያደነ ሥጋ ያበላው ነበር።ርብቃ ግን ያዕቆብን ትንን ነበር። 29 ለዕለታት አንድ ቀን ያዕቆብ ቀይ የምስር ወጥ በመሥራት ላይ እንዳለ ዔሳው ከአደን መጣ፤ በጣም እርቦት ነበር፤ 30 ስለዚህም ያዕቆብ "ከዚህ ከቀይ ወጥ ሰጠኝ" አለው። ኤዶም የተባለውም ነዚሁ ምክንያት ነበር። 31 ያዕቆብም "በመጀመሪያ ብኩርናህን ሽጥልኝ" አለው። 32 ዔሳውም "እኔ በረሀብ መሞቴ ነው፤ ታዲያ ብኩርና ምን ያደርግልኛል?" አለው። 33 ያዕቆብም "እንግዲያውስ ብኩርናህን እንደምትሸጥልኝ መጀመሪያ ማልልኝ" አለው። ስለዚህ ዔሳው ምሎ ብኩርናውን ለያዕቆብ ሸጠ። 34 ከዚህ በኋላ ያዕቆብ የምስሩን ወጥ በእንጀራ አድርጎ ሰጠው፤ ዔሳውም ከበላና ከጠጣ በኋላ ተነሥቶ ሄደ፤ በዚህ ዐይነት ዔሳው ብኩርናውን በመናቅ አቃለላት።



Chapter 26

1 በአብርሃም ዘመን ከደረሰው ረሀብ ሌላ ዳግመኛ ረሀብ በምድር ላይ መጣ፤ በዚህ ምክንያት ይስሐቅ የፍልስጥኤማዋን ንጉሥ አቢሜሌክ ወዳለበት ወደ ገራር ሄደ፤ 2 በዚህም እግዚአብሔር ለይስሐቅ ተገለጠለትና እንዲህ አለው፣ "ወደ ግብፅ አገር አትሂድ፤ እንድትኖርበትም በምነግርህ በዚህ ምድር ተቀመጥ፤ 3 እዚሁ ኑር፤ እኔም ከአንተ ጋር እሆናለሁ፤ እባርክሃለሁ፤ ይህም ምድር ለአንተና ለዝርይዎችህ እሰጣለሁ፤ በዚህ ዐይነት ለአባትህ ለአብርሃም የገባሁትን ቃል ኪዳን እፈፅማለሁ፤ 4 ዘርህን አንደ ሰማይ ክዋክብት አበዛዋልለሁ፤ ይህንንም ሁሉ ምድር አወርሳቸዋለሁ፤ ይህንንም ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ። 5 አንተን የምባርክበትንም ምክንያት አባትህ አብርሃም ለእኔ ታዛዥ በመሆን የሰጠሁት ሕግና ሥርዓት ሁሉ ስለ ጠበወ ነው። 6 ስለዚህ ይስሐቅ መኖሪያውን በገራር አደረገ፤ 7 በዚያ አገር ስሰዎችም ስለ ርብቃ "ምንህናት" ብለው በጠየቁት ጊዜ "እኅቴ ናት" አላቸው፤ ይህንንም ያለበት ምክንያት ርብቃ በጣም ቆንጆ ስለ ነበረች የዚያ አገር ሰዎች በእርስዋ ሰበብ እንዳይገድሉት በመፍራት ነው። 8 ይስሐቅ እዚያ አገር ብዙ ጊዜ ከቆያ በኋላ የፍልስጥኤም ንጉሥ አቢሜሌክ በመስኮት ወደ ውጪ ሲመለከት ይስሐቅና ርብቃ እንደባልና ሚስት በመዳራት ሲጫወቱ አየ። 9 ስለዚህ አቢሜሌክ ይስሐቅን አስጠርቶ "ለካስ ርብቃ ሚስትህ ናት! ታዲያ "እኅቴ ናት' ያልከው ለምንድን ነው?" ሲል ጠየቀው። እርሱም "ሚስቴ ነች ያልኩ እንደሆን ሰዎች ይገድሉኝል ብዬ አስፈራሁ ነው" ብሎ መለሰ። 10 አቢሜሌክ "ይህ በእኛ ላይ ያደረግኸው ነገር ምንድን ነው? ከእኛ ሰዎች አንዱ በቀላሉ ሚስትህን ለመድፈር በቻለ ነበር፤" 11 ቀጥሎም አቢሜሌክ "ይህን ሰው ወይም ሚስቱን የሚነካ ሰው በሞቱ ይቀጣል"የሚል ማስጠንቀቂያ ለሕዝቡ ሰጠ። 12 ይስሐቅ በዚያች ምድር ዘርን ዘራ፤ እግዚአብሔር ስለባረከውም በዚያኑ ዓመት መቶ እጥፍ አመረተ፤ 13 ሀብት በሀብት ላይ እየተጨመረበት ዘመን የእርሱ አገልጋዮች ቁፍረዋቸው የነበሩትን የውሃ ጉድጓዶች ሁሉ ዐፈር ሞልተው ደፈኑአቸው። 14 ብዙ የበግና የከብት መንጋ፤ እንዲሁም ብዙ አገልጋዮች ስለ ነበሩት ፍልስጥኤማውያን ቀኑበት። 15 ስለዚህ የይስሐቅ አባት አብርሃም በሕይወት በነበረበት ዘመን የእሱን አገልጋዮች ቁፍረዋቸው የነበሩትን ውሃ ጉድጓዶች ሁሉ ዐፈር ሞልተው ደፈኑአቸው። 16 በዚያን ጊዜ አቢሜሌክ ይስሐቅን "ኅይልህ ከእኛ ይልቅ እየበረታ ስለሄደ፤ አገራችንን ለቀህ ውጣ" አለው። 17 በዚህ ምክንያት ይስሐቅ ያንን ቦታ ለቆ በገራር ሸለቆ ውስጥ ሰፈረ፤ እዚያም ተቀመጠ። 18 አብርሃም በሕይወት ሳለ አስቆፍሮአቸው የነበሩትን አብርሃም ከሞተ በኋላ ግን ፍልስጥኤማውያን የደፈኑአቸውን የውሃ ጉድጓዶች ይስሐቅ እንደገና እንዲቆፍሩ አደረገ፤ አባቱ ባወጣላቸ ስሞችም ጠራቸው። 19 የይስሐቅ አገልጋዮች በሸለቆው ውስጥ የውሃ ጉድጓድ ቁፍሩና ጥሩ የምንጭ ውሃ አገኙ፤ 20 የገራር እረኞች ግን "ይህ ውሃ የእኛ ነው" በማለት ከይስሐቅ እረኞች ጋር ተጣሉ።በዚህ ምክንያት ይስሐቅ ጉድጓዱን "ዔሤቅ" ብሎ ሰየመው። 21 የይስሐቅ አገልጋዮች ሌላ የውሃ ጉድጓድ ቁፈሩ፤ በዚህኛውም ጉድጓድ ምክንያት ሌላ ጠብ ተነሣ፤ ስለዚህ ይስሐቅ ይህን ጉድጓድ "ስጥና" ብሎ ሰየመው። 22 ከዚያም እልፍ ብሎ ሌላ የውሃ ጉድጓድ ምክንያት ምንም ጠብ ስላልተናሳ "እነሆ አሁን እግዚአብሔር ሰፊ ቦታ ሰጠን፤ በምድር ላይም እንበዛለን ሲል ያንን ቦታ 'ረሖቦት" ብሎ ሰየመው። 23 ከዚያ በኋላ ይስሐቅ ወደ ቤርሳቤህ ወጣ፤ 24 በዚያን ሌሊት እግዚአብሔር ተገለጠለትና "እኔ የአባትህ አምላክ ነኝ፤እኔ ከአንተ ጋር ስለሆንኩ አትፍራ! ለአገልጋዬ ለአብርሃም በገባሁት ቃል ኪዳን መሠረት እባርክሃለሁ፤ ዘርህንም አበዛዋለሁ" አለው። 25 ይስሐቅ በዚያ መሠዊያ መሠዊያ ሠራና ለእግዚአብሔር ሰገደ፤ መኖሪያውንም እዚያ አደረገ፤ አገልጋዮቹም ሌላ ጉድጓድ ቆፈሩ። 26 አቢሜሌክ ከአማካሪው ከአሑዘትና ከሠራዊቱ ኣዥ ኮፊኮል ጋር ይስሐቅን ለመጎብኘት ከገራር ወት፤ 27 ስለዚህ ይስሐቅ "ከዚህ በፊት ጠልታችሁን አገራችሁ እንድወጣ አድርጋችሁኛል፤ ታዲያ አሁን ልትጎበኝ የመጣችሁት ለምንድን ነው?" አላቸው። 28 እነርሱም እንዲህ ሲሉ መለሱለት፣ "እግዚአብሔር ከአንተ ጋር መሆኑን በግልጥ ዐውቀናል፤ ስለዚህ በእኛና በአንተ መካከል በሰላም ለመኖር የሚያስችል ስምምነት በመሐላ ለመፈፀም አስበናል፤ በዚህም መጀረት ቃል ኮዳን እንድትገባልን የሚንፈለገው፣ 29 በእኛ ላይ ምንም ዐይነት በደል እንዳታደርስብን ነው፤ ምክንያቱም እኛ በአንተ ላይ ምንም ግፍ አልሠራንም፤ ዘውትር መልካም ነገር አደረግንልህ እንጂ ክፉ አላደረግብህም፤ ከአገራችንም የወጣኸው በሰላም ነው፤ አሁንም እግዚአብሔር ባርኮሃል።" 30 ከዚህ በኋላ፣ ይስሐቅ ግብዣ አደረገላቸው፤ እነሱም በሉ፣ ጠጡ። 31 በማግሥቱ ጠዋት በማለዳ ተነሡና ተማማሉ፤ ይስሐቅ ካሰናበታቸው በኋላም በሰላም ሄዱ። 32 ከዚያኑ ቀን የይስሐቅ አገልጋዮች መጥተው ስለ ቁፈሩት ጉድጓድ ለይስሐቅ ነገሩት፤ "ውሃ አገኘን" ብለውም አበሠሩት። 33 እርሱም የውሃን ጉድጓድ "ሳቤህ"ብሎ ጠራው፤ ስለዚህም የከተማይቱ ስም እስከ ዛሬ "ቤርሳቤህ" እየተባለ ይጠራል። 34 ዔሳው አርባ ዓመት ሲሆንው የብኤሪን ልጅ ዮዲትንና የኤሎንን ልጅ ባሴማትን አገባ፤ ሁለቱም ሒታውያን ነበሩ። 35 ይህም ጋብቻ ይስሐቅንና ርብቃን ሲያዝናቸው ይኖር ነበር።



Chapter 27

1 ይስሐቅ አርጅቶ ዐይኖቹም ታውረው ነበር፤ ታላቁ ልጁን ዔሳውን፤ "ልጄ ሆይ!" ብሎ ጠራው፤ ልጁም "እነሆ አለሁ" አለ። 2 ይስሐቅም እንዲህ አለው፣ "እንደምታየኝ አርጅቻለሁ፤ የምሞትበትንም ቀን አላውቅም፤ 3 ስለዚህ የምታድንበትን ቀስትና ፍላጻ ያዝ፤ ወደ ዱር ሂድና አውሬ አድነህ ሥጋ አምጣልኝ፤ 4 ልክ እንደምወደው አድርገህ ምግብ ሥራልኝ ከበላሁም በኋላ ከመሞቴ በፊት የመጨረሻ ምርቃቴን እሰጥሃለሁ።" 5 ይስሐቅ ለልጁ ለዔሳው ወደ አደን ከሄደ በኋላ፣ 6 ርብቃ ልጅዋን ያዕቆብን "አባትህ ዔሳውን እንዲህ ሲለው ሰማሁ፣ 7 አውሬ አድነህ ሥጋ አምጣልኝ፤ ልክ እንደምወደው አድርገህ የጣፈጠ ምግብ ሥራልኝ፤ ሳልሞትም በእግዚአብሔር ፊት እነርቅሃለሁ፤ 8 አሁንም ልጄ ሆይ! የምነግርህን አድምጥ፤ የማዝህንም አድርግ፤ 9 አባትህ እንደሚወደው አጣፋጩ ጥሩ ምግብ እንድሠራለት፣ ወደ መንጋዎች ሂድና ሁለት የሰቡ የፍየል ጥቦቶች አምጣልኝ፤ 10 አንተም ያዘጋጀሁትን ምግብ እንዲበላ ለአባትህ ወስደህ ታቀርብለታለህ፤ በዚህ ዐይነት አባትህ ከመሞቱ በፊት ይመርቅሃል።" 11 ያዕቆብ ግን እናቱን ርብቃን "የወንድሜ የዔሳው ገላ ጠጉራም ነው፤ የ እኔ ገላ ግን ምንም ጠጉር የሌለው ለስላሳ ነው፤ 12 ምናልባት አባቴ ቢዳስሰኝና እንዳታለልኩህ ቢያውቅ በምርቃት ፈንታ እርግማን እንደማተርፍ ታውቂ የለምን?" አላት። 13 እናቱም "ልጄ ሆይ! የአንተ እርግማን በእኔ ላይ ይሁን፤ አሁንም እንደነገርሁህ አድርግ፤ ሄድህ ጥቦቶቹን አምጣልኝ" አለችው። 14 ስለዚህ ሄዶ ጥቦቶቹን አመጣለት እርስዋም ልክ አባቱ እንደሚወደው እድርጋ ጥሩ ወጥ ሠራች፤ 15 የታላቁ ልጅዋን የዔሳውን የክት ልብስ ከተቀመጠበት ቦታ አውጥታ ለያዕቆብ አለበሰችው። 16 የፍየሎቹንም ቆዳ በክንዶቹ ላይና ጠጉር በሌለበት በአንገቱ ላይ አለበሰችው። 17 ያዘጋጀውንም ጥሩ ወጥ ከጋገረችው እንጀራ ጋር ልልጅዋ ለያዕቆብ ሰጠችው። 18 ያዕቆብ ወደ አባቱ ሄደና "አባባ!" አለው፤ እርሱም "እነሆ አለሁ! ለመሆኑ አንተ የትኛው ልጄ ነህ!" አለ። 19 ያዕቆብም "የበኩር ልጅህ ዔሳው ነኝ፤ እነሆ እንዳዘዝከኝ አድርጌአለሁ፤ እንድትመርቀኝ እስቲ ቀና በልና ያመጣሁልህን የአደን ሥጋ ተመገብ" አለው። 20 ይስሐቅም "ልጄ ሆይ! እንዴት ቶሎ ልታገኝ ቻልህ?" አለው። ያዕቆብም "አምላክህ እግዚአብሔር ስለረዳኝ በቶሎ ለማግኘት ቻልሁ" አለው። 21 ይስሕቅም "እስቲ ወደ እኔ ቀረብ በልና ልዳብስህ፤ በእርግጥ አንተ ዔሳው ነህን?" አለው። 22 ያዕቆብም ወደ አባቱ ተጠጋ፤ አባቱም ዳሰሰውና "ድምፅህ የያዕቆብ ድምፅ ይመስላል፤ ክንድህ ግን የዔሳውን ክንድ ይመስላል" አለው። 23 ክንዶቹ እንደ ዔሳው ክንዶች ጠጉራም ስለ ነበሩ ይስሐቅ ያዕቆብን ለይቶ ማውቅ አልቻለም፤ ሊመርቀው ከዝዘጋጀ በኋላ፣ 24 "እርግጥ አንተ ልጄ ዔሳው ነህን?" ሲል እንደገና ጠየቀው፤ እርሱም "አዎ ነን" አለ። 25 ይስሐቅም "ልጄ! በል ከአደንከው ሥጋ አቅርብልኝ፤ ከበላሁም በኋላ እመርቅህለሁ" አለው። ያዕቆብም ምግቡን አቀረበለት፤ የወይን ጠጅም እንዲጠጣ አመጣለት። 26 ከዚህ በኋላ አባቱ ይስሐቅ "ልጄ ሆይ! ቀረብ በልና ሳመኝ" አለው፤ 27 ያዕቆብም ቀርቦ ሳመው። ይስሐቅ የያዕቆብ ልብስ ባሸተተ ጊዜ እንዲህ ሲል መረቀው፣ "እነሆ የልጄ መልካም ሽታ እግዚአብሔር እንደባረከው የእርሻ ሽታ ነው፤ 28 እግዚአብሔር ከሰማይ የሚያረሰርሰው ተል ይስጥህ፤ ምድርህን ያለምልምልህ፤ እህልንና የወይን ጠጅህን ያብዛልህ፤ 29 መንግሥታት ይገዙልህ፤ ሕዝቦችህም ያገልግሉህ፤ በወንድሞችህ ሁሉ ላይ አለቃ ሁን፤ የእናትህም ልጆች ይስገዱልህ፤ የሚረግሙህ የተረገሙ ይሁኑ፤ የሚመርቁህ የተመረቁ ይሁኑ።" 30 ይስሐቅ ያዕቆብን መርቆ እንዳበቃና ያዕቆብም አባቱን ፊት እንደወጣ ወዲያውኑ ዔሳው ከአደን ተመልሶ መጣ። 31 እርሱም በበኩሉ የጣፈጠ ወጥ ሠርቶ ለአባቱ አቀረበለትና "አባቴ ሆይ እንድትመርቀኝ፣ እስቲ ቀና ብለህ ካመጣሁልህ የአደን ሥጋ ብላ" አለው። 32 ይስሐቅም 'አንተ ማን ነህ?" አለው፤ እርሱም "እኔ የበኩር ልጅ ዔሳው ነኝ" አለ። 33 ይስሐቅም እጅግ ደንግጦ እየተነቀጠቀጠ "ታዲያ አውሬ አድኖ ያመጣልኝ ማን ነበረ? ልክ አንተ ከመምጣትህ በፊት ተመገብሁ የመጨረሻ ምርቃቴንም ሰጠሁት፤ ምርቃቱም ተእርሱ ሆኖ ይኖራል"አለው። 34 ዔሳው ይህን በሰማ ጊዜ ድምፁን ከፍ በማድረግ ምርር ብሎ እያለቀሰ "አባቴ ሆይ! እኔንም መርቀኝ!" አለ። 35 ይስሐቅም "ወንድምህ መጥቶ እኔን በማታለል የአንተን ምርቃት ወስዶብሃል"አለው። 36 ዔሳውም "እርሱ እኔን ሲያሰናክለኝ ይህ ሁለተኛው ነው፤ ያዕቆብ መባሉ ተገቢ ነው፤ ከዚህ በፊት ብኩርናዬን ወሰደብኝ፤ አሁን ደግሞ ምርቃቴን ቀማኝ፤ ታዲያ ለእኔ ያስቀረከው ምንም ምርቃት የለምን? አለው። 37 ይስሐቅም "ቀድሞ ብዬ እርሱን የአንተ ጌታ አድርጌዋለሁ፤ ወንድሞቹ ሁሉ የእርሱ አገልጋዮች እንዲሆኑ አድርጌአለሁ፤ እህልና የወይን ጠጅ እንዲበዛለት አድርጌአለሁ፤ ልጄ ሆይ! እንግዲህ ለአንተ ምን ላደርግልህ እችላለሁ?" አለው። 38 ዔሳውም "አባቴ ሆይ! ምርቃትህ እንዲት ብቻ ናትን? እባክህ እኔንም መርቀኝ" እያለ ለማልቀስ አባቱን ነዘነዘው። 39 ይስሐቅም አንዲህ አለው። "በረከት ከሞላበት ለምለም ምድር ርቀህ ትኖራለህ፤ የሰማይ ጠልም አታገኝም፤ 40 በሰይፍም ኅይል ትኖራለህ፤ የወንድምህም አገልጋይ ትሆናለህ፤ በተቃወምከውም ጊዜ ግን ከእርሱ ጭቁና ትላቀቃለህ።" 41 አባቱ ስለመረቀው ዔሳው ያዕቆብን አጥብቆ ጠላው፤ በልቡም "አባቴ በቅርብ ቀን ይሞታል፤ ከዚህ በኋላ ወንድሜን ያዕቆብን እገድለዋለሁ"ብሎ አሰበ። 42 ነገር ግን ርብቃ የዔሳውን ዕቅድ ስለ ሰማች፣ ያዕቆብን ጠርታ እንዲህ አለችው፣ "አድምጠኝ፤ ወንድምህ ዔሳው አንተን በመግደል ሊበቀልህ አስቦአል፤ 43 አሁንም ልጄ ሆይ! የምልህን አድርግ፤ ተነሥተህ በካራን ወደሚገኘው ወደ ወንድሜ ወደ ላባ ሽሽ፤ 44 የወንድምህ ቁጣ እስኪበርድ ድረስ ለጥቂት ጊዜ እዚያው ቆይ፤ 45 ቁጣውም ሲበርድ ያደረግህበትን ነገር ይረሳል፤ ከዚያ በኋላ ሰው ልኬ አስመጣሃለሁ፤ ሁለታችሁም በአንድ ቀን ማጣት አልፈልግም። 46 ርብቃ ይስሐቅን "ዔሳው ባገባቸው በእነዚህ በሖታውያን ሴቶች ምክንያት መኖሬን ጠላሁት፤ ያዕቆብ ደግሞ ከነዚህ ከሒታውያን ሴቶች አንዲቱ ከገባ ለመኖር ይልቅ ሞቴን እመርጣለሁ"አለችው።



Genesis 27:1

ዓይኖቹ ደክመው

ይህ የሚናገረው ዓይኖች እንደ መብራት ብርሃን እየቀነሱ እንደሄዱ እና ማየት ወደ መሳን ደረጃ እንደደረሱ ነው:: አት: “ዓይኖቹ ማየት ተስኖአቸው” ወይም “ዓይኖቹ ወደ መታወር ደርሰው” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)::

እርሱም እርሱን አለው

“ዔሣው መለሰለት”“ዔሣው መለሰለት”

እነሆ አለው

“እነሆ አለሁ” ወይም “እየሰማሁ ነኝ” በዘፍጥረት 22:1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

እርሱም አለው

“ከዚያም ይሥሐቅም አለ”

ይሄው ተመልከት

“ይኼው ተመልከት” የሚለው ሀረግ ለሚቀጥለው ሃሳብ አጽንዖት የሚሰጥ ነው:: አት: “በጥንቃቄ ስማ ግምታዊ እውቀት” ወይም “ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ”

የምሞትበትን ቀን አላውቅም

ይህ ይስሐቅ ቅርብ ጊዜ እንደሚሞት የሚያመለክት ነው:: አት: “ከማንኛውም ጊዜ ሊሞት ይሆናል”:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሞት

አካላዊ ሞትን ይገልጻል

Genesis 27:3

አጠቃላይ መረጃ

“ይስሐቅ ለታላቅ ልጁ ለዔሣው መመሪያልችን ይሰጣል”

የአደን መሣሪያህን

“የአደን መሣሪያዎችህን”

የፍላጻ ኩሮጆ

የፍላጻ ኩሮጆ የቀስቶች መሸከሚያ ነው:: አት: “የቀስቶች መሸከሚያ ኩሮጆ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አድነህም አምጣልኝ

“የዱር እንስሳት አድነህ አምጣልኝ”

የምወደው ዓይነት ጣዕም ያለው ምግብ አዘጋጅተህ

“ጣዕም ያለው” የሚለው ቃል እጅግ በጣም ጣፋጭ የሆነውን ነገር ያመለክታል:: አት: “የምወደው ዓይነት የሥጋ ምግብ አዘጋጅልኝ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

እንዲመርቅህ

በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን አባት መደበኛ የሆነ መንገድ ልጆችን ይመርቃል

Genesis 27:5

“በወቅቱ”

በወቅቱ የሚለው ቃል ትኩረቱ ወደ ርብቃና ያዕቆብ መዞሩን ያሳያል:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ርብቃም ይስሐቅ ለልጁ ለዔሣው ሲነግር ትሰማ ነበር

“ይስሐቅ ለልጁ የተናገረውን ርብቃ ትሰማ ነበር”

ዔሣው … ለማምጣት ሄደ:: ርብቃም ያዕቆብን እንዲህ አለችው

ዔሣው ከወጣ በኋላ ርብቃ የሰማችውን ለያዕቆብ ተናገረች:: አት: “ዔሣው ለማምጣት በወጣ ጊዜ ርብቃም ለያዕቆብ ተናገረች” (አያየዥ ቃላት ይመልከቱ)

ለዔሣው ለልጁ …. ለያዕቆብ ልጅዋን

ዔሣውና ያዕቆብ ሁለቱም የይስሐቅና የርብቃ ልጆች ናቸው አንድ ወላጅ አንዱን ልጅ ከሌላኛው ልጅ አብልጦ እንደሚወድ ተደርገው የእርሱ ልጅ እና የእርስዋ ልጅ ተብለው ተጠርተዋል::

ይሄው ተመልከት

“ይኼው ተመልከት” የሚለው ሀረግ ለሚቀጥለው ሃሳብ አጽንዖት የሚሰጥ ነው:: አት: “በጥሞና ስማ ግምታዊ እውቀት” ወይም “ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ”

እርሱም አለ ከመሞቴ በፊት በእግዚአብሔር ፊት እንዲመርቅህ ጥሩ ጣዕም ያለው ምግብ እንድበላ አዘጅልኝ

ይህ በጥቅስ ውስጥ የሚገኝ ጥቅስ ነው:: እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል አት: “ለዔሣውም ነገረው; ‘የዱር እንስሳ እንዲያድንና የሚወደውን ጣዕም የሥጋ ምግብ እንዲያዘጋጅለት’ ከዚያም ከመሞቱ በፊት በእግዚአብሔር ፊት የስሐቅ ዔሣውን እንዲባርከው” (በጥቅስ ውስጥ ጥቅሶችንና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)::

አድነህም አምጣልኝ

“የዱር እንስሳት አድነህ ገድለህ አምጣልኝ”

የምወደው ዓይነት ጣዕም ያለው ምግብ አዘጋጅተህ

“የምወደው ዓይነት የሥጋ ምግብ አዘጋጅልኝ” ይህን በዘፍጥረት 27:4 እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

በእግዚአብሔር መገኘት እንዲመርቅህ

“በእግዚአብሔር ፊት እንዲመርቅህ”

Genesis 27:8

አጠቃላይ መረጃ

ርብቃ ለሁለተኛ ልጅዋ ለያዕቆብ መናገርዋን ቀጠለች

አሁንም

ይህ በዚያ ወቅት የሚለውን የሚናገር አይደለም ነገር ግን ለሚቀጥለው ዋና ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ነው::

እኔ በማዝዝህን ድምጼን ስማኝ

ርብቃ “ድምጼን” ያለችው የምትናገረውን ነገር ለማመልከት ነው:: አት: “ታዘዘኝ የምናገረውንም ነገር አድርግ” (ተዛማጅ ባሕሪይ የሚገልጽ ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

እነርሱንም አባትህ እንደሚወደው ዓይነት ጣፋጭ ምግብ አዘጋጅለታለሁ

ጣፋጭ የሚለው ቃል በጣም ጥሩ ጣዕም ያለውን ነገር ያመለክታል:: በዘፍጥረት 27:4 ተመሳሳይ ቃል እንዴት እንደተተረጐመ ይመልከቱ::

ወደ አባትህም ይዘህ ግባለት

“ከዚያም ወደ አባትህ ይዘህ ግባ”

እንዲበላ እንዲመርቅህ

ከበላ በኋላ ይመርቅሃል

ይመርቅህ ይሆናል

ምርቃት የሚለው ቃል አባት ልጆቹን የሚናገረው መደበኛ ምርቃት ነው

ከሞቱ በፊት

ከመመቱ በፊት

Genesis 27:11

እኔ ለስላሣ ነኝ

“የእኔ ገላ ለስላሣ ነው” ወይም “እኔ ጸጉራም አይደለሁም”

በምርቃት ፈንታ ርግማን አተርፋለሁ

መረገም ወይም መባረክ ምርቃት ወይም በረከት በአንድ ሰው ላይ እንደሚሆን ዕቃ ተደርገው ተነግረዋል አት ከዚያም ከዚህም የተነሣ ይረግመኛል ወይም አይባርከኝም (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 27:13

ልጄ ሆይ ማንኛውም ርግማን በእኔ ላይ ይድረስ

“ልጄ ሆይ መርገምህ በእኔ ላይ ይሁን” መረገም ርግማን በአንድ ሰው ጫንቃ ላይ እንደሚሆን ዕቃ ተደርጐ ተገለጾአል:: አት “ልጄ ሆይ አባትህ አንተን ከመርገም እኔን ይርገመኝ” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ድምጼን ታዘዝ

ርብቃ “ድምጼን” ያለችው የምትናገረውን ነገር ለማመልከት ነው:: አት: “የሚናገርህን ታዘዝ” ወይም “ታዘዘኝ” (ተዛማጅ ባሕሪይ የሚገልጽ ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

እነርሱን አምጣልኝ

“ጠቦቶቹን አምጣልኝ”

ልክ አባቱ እንደሚወደው ዓይነት ጣፋጭ ምግብ አዘጋጀችለት::

ጣፋጭ የሚለው ቃል በጣም ጥሩ ጣዕም ያለውን ነገር ያመለክታል:: በዘፍጥረት 27:4 ተመሳሳይ ቃል እንዴት እንደተተረጐመ ይመልከቱ::

Genesis 27:15

ጠቦቶቹን ቆዳ በእጆቹ ላይ አለበሰችው

የጠቦቶች ቆዳዎች ጸጉር ነበረባቸው

የሠራችውን ጣፋጭ መብልና እንጀራውን ለልጅዋ ለያዕቆብ በእጁ ሰጠችው

“የሠራችውን ጣፋጭ መብልና እንጀራውን ለልጅዋ ለይዕቆብ ሰጠችው”

Genesis 27:18

እርሱም አለው

“እናም አባቱ መለሰው” ወይም “ይስሐቅም መለሰው”

አነሆኝ

“አዎን እየሰማሁ ነኝ” ወይም “አዎን ምንድነው?” በዘፍጥረት 22 1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

የተናገርከኝ ወይም ያዘዝከኝን አድርጌአለሁ

እንዳደርገው የነገርከኝን አድርጌአለሁ

አደን አድኜ ካመጣሁት ከፊሉ

“የታደነ” የምለው ቃል አንድ ሰው የዱር እንሰሳትን አድኖና ገድሎ የሚያቀርበውን ያመለክታል:: በዘፍጥረት 27:3 “የታደነ” የሚለው እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Genesis 27:20

እርሱም አለው

ያዕቆብም መለሰው

አሳካልኝ

ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር እግዚአብሔር ለሁኔታው ምክንያን እንደሆነ ይገልጻል:: አት: “በማድንበት ጊዜ እንዲሳካልኝ ረድቶኛል” (ፈሊጣዊ አነጋገሮች ይመልከቱ)::

በእርግጥ እውነተኛው ልጄ ዔሣው መሆንህን

“በእርግጥ ልጄ ዔሣው መሆንህን”

Genesis 27:22

ያዕቆብ ወደ አባቱ ወደ ይስሐቅ ቀረበ

“ያዕቆብ ወደ አባቱ ወደ ይስሐቅ ተጠጋ”

ይህ ድምጽ የያዕቆብ ድምጽ ነው

እዚህ ይስሐቅ የያዕቆብ ድምጽ ያዕቆብን እንደሚወክል ይናገራል፡፡ አት፡ “ድምጽህ የያዕቆብ ይመስላል” (ክፍልን እንደ ሙሉ ወይም ሙሉውን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እጆቹ ግን የዔሣው እጆች ናቸው

እዚህ ይስሐቅ የዔሣው እጆች ዔሣውን እንደሚወከሉ ይናገራል፡፡ አት፡ እጆች ግን የኤሣው እጆች እንደሆኑ ይሰሙኛል፡፡ (ክፍልን እንደ ሙሉ ወይም ሙሉውን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 27:24

እርሱም አለ

ይስሐቅ ልጁን ከመባረኩ በፊት ይህን ጥቃቄ ይጠይቀዋል:: አት፡ “ነገር ግን መጀመሪያ ይስሐቅ ጠየቀው” (የክስተቶች ቅደም ተከተል ይመልከቱ)

አድነህ ካቀረብክልኝ ልብላ

የታደነ የሚለው ቃል ሰዎች አድነውና ገድለው የሚያቀርቡትን የዱር እንሰሳ ያመለክታል:: በዘፍጥ 27:7 የታደነ እንዴት አንደተተረጐመ ይመልከቱ::

ጠጣም

“ይስሐቅ ጠጣ”

Genesis 27:26

እርሱም ልብሶቹን ካሸተተ በኋላ መረቀው

ልብሶች የኤሣው ልብሶች ሽታ እንዳሸቱ ግልጽ ነው:: አት: “እርሱም ልብሶቹን አሸተተ እናም ሽታው እንደ ዔሣው ልብሶች ሽታ ስለሆነ ባረከው” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አሸተተ

ይስሐቅ አሸተተ

ሽታ

ጠረን

ባረከው

“ከዚያም ባረከው” ይህ አባት ልጆቹን የሚባረከውን መደበኛ በረከት ያመለክታል::

እነሆ የልጄ ጠረን

“እነሆ” የሚለው ቃል ይህ እውነት ነው የሚለውን ለመግለጽ የተጠቀመ አበክሮአዊ ሥዕላዊ አገላለጽ ነው:: አት: “በእውነት የልጄ ጠረን”

እግዚአብሔር እንደባረከው

እዚህ በረከት የሚለው ቃል እግዚአብሔር በእርሻው መልካም ነገሮች እንዲሆኑና ፍሬያማ እንዲሆን እንዲያደርግ ነው:: አት: “ያም እግዚአብሔር ፍሬያማ እንዲያደርግ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 27:28

አጠቃላይ መረጃ

ይህ የይስሐቅ ባረኮት ነው ለኤሳው የተናገረው መሰለሙ ነገር ግን የተናገረው ለያዕቆብ ነው

ይስጥህ

እዚህ “ይስጥህ” ነጠላና ያዕቆብን የሚያመለክት ነው በረከቱ ግን ለያዕቆብ ትውልድም የሚሆን ነው:: (ሁለተኛ ሰው አጠቃቀምንና ክፍልን እንደ ሙሉ እና ሙሉን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

የሰማይን ጠል

ጠል በሌሊት በተክሎች ላይ የሚሆን የውሃ ጠብታ ነው:: በትርጉም ይህን ግልጽ ማድረግ ይቻላል:: አት: “ተክሎችዎን ለማጠጣት የሌሊት ጠል” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የምድርንም በረከት

ለም መሬት የመኖር መሬት ስብና ሀብታም እንደሆነች ተደርጐ ተገለጾአል:: አት: “እህልን የሚያመርት መልካም መሬት ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ”

የተትረፈረፈ እህልና አዲስ የወይን ጠጅ

“እህል”ና “ወይን” ያልተገለጹ እስከሆነ ድረስ ጠቅለል ባለ መልክ መግለጽ ይቻላል:: አት: “የተትረፈረፈ መብልና መጠጥ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 27:29

አንተ…. ያንተ

እዚህ እነዚህ ተውላጤ ስሞች በነጠላ የተገለጹና የዕቆብን ያመለክታሉ በረከቱ ግን ለያዕቆብ ትውልድም ነው (ሁለተኛ ሰው አገላለጽንና ክፍልን እንደ ሙሉ እና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ሕዝቦች ተደፍተው እጅ ይንሡህ ወይም ይስገዱልህ

እዚህ ሕዝቦች ሰዎችን ያመለክታል አት የሁሉም ሕዝቦች ሰዎች ተደፍተው እጅ ይንሡህ:: (ተዛማጅ ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ይስገዱልህ

ይህ ጐንበሥ በማለት አንድ ሰው አክብሮት መስጠትን ይገልጻል ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ

የወንድሞችህ ጌታ ሁን

በወንድምችህ ላይ ጌታ ወይም ገዢ ሁን

ወንድሞችህ …የእናትህም ልጆች

ይስሐቅ ይህን በረከት በቀጥታ ለያዕቆብ ይናገራል ነገር ግን ይህ የያዕቆብ ትውልድ በኤሣው ትውልድና በሌሎች ማናቸውም የያዕቆብ ወንድሞች ትውልድ ላይ ገዢዎች እንደሚሆኑ ለእነርሱም ይሆናል፡፡ (ክፍል ለሙሉና ሙሉን ለክፍል የመጠቀም አገላለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

የእናትህም ልጆች ይስገዱልህ

የእናትህም ልጆች የሰግዱልሃል

የምረግሙህ የተረገሙ ይሁኑ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “እግዚአብሔር የሚረግሙህን ሁሉ ይርገማቸው“ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የሚባርኩህ የተባረኩ ይሁኑ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “እግዚአብሔር የሚባርኩህን ሁሉ ይባርካቸው“ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 27:30

ያዕቆብም ገና ከአባቱ ዘንድ ሳይወጣ ወዲያውኑ

“ከአባቱን ከይስሐቅን ድንኳን እንደወጣ”

ጣፋጭ ምግብ

የምወደው ጣፋጭ ሥጋ በዘፍጥረት 27፡3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ልጅህ ካደንሁት

እዚህ “ልጅህ” ኤሣው ካደነው ያዘጋጀውን ምግብ በትህትና ያቀረበበት መንገድ ነው:: (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ልጅህ ካደነው

የታደነ የሚለው ቃል ሰዎች አድነውና ገድለው የሚያቀርቡትን የዱር እንሰሳ ያመለክታል:: በዘፍጥ 27:7 የታደነ እንዴት አንደተተረጐመ ይመልከቱ::

ባርከኝ

ይህ አንድ አባት ልጆቹን የሚባርክበት መደበኛ መንገድ ያመለክታል

Genesis 27:32

ለእርሱም አለው

ዔሣውን አለው

ይስሐቅም ተንቀጠቀጠ

ይስሐቅም መንቀጥቀጥ ጀመረ

በአደን የታደነ

የታደነ የሚለው ቃል ሰዎች አድነውና ገድለው የሚያቀርቡትን የዱር እንሰሳ ያመለክታል:: በዘፍጥ 27:7 የታደነ እንዴት አንደተተረጐመ ይመልከቱ::

Genesis 27:34

ድምጹን ከፍ በማድረግ ምርር ብሎ አለቀሰ

የዔሣው ምሬት አንድ መራራ ጣዕም ካለው ነገር ጋር የሚመሳሰል ነበር:: አት: “በከፍተኛ ድምጽ አለቀሰ” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ምርቃትህን ወስዶብሃል

ይህ ያዕቆብ የዔሣውን በረከት እንደወሰደ የሚገልጽ ምሳሌያዊ አገላለጽ ነው አት በአንተ ፈንታ እርሱን ባርከአለሁ (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 27:36

ያዕቆብ መባሉ የሚታወቅ አይደለምን?

ዔሣው በያዕቆብ ላይ ያለውን ቁጣ ለመጨመር ጥያቄ ይጠቀማል:: አት ያዕቆብ በእርግጥ ለወንድሜ ትክክለኛ ስም ነው:: (ቅኔያዊ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ያዕቆብ

ተርጓሚዎች እንዲህ የሚለውን የግርጌ ማስታወሻ ይጠቀማሉ ያዕቆብ የሚለው ስም ተረከዙን ያዘ የሚል ትርጉም አለው በመሠረታዊው ቋንቋ ቃሉ አታላይ የሚል አንድምታ አለው::

ብኩርናዬን ወሰደብኝ

ይህ ብኩርና እንደ አንድ ዕቃ ከሰው እንደሚወሰድ አድርጐ ይናገራል:: አት: “የእኔ የሆነው ብኩርና በማታለሉ ምክንያት የእርሱ ሆኖአል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)::

አሁን ደግሞ ምርቃቴን ቀማኝ

ይህ ምርቃት እንደ አንድ ዕቃ ከሰው እንደሚቀማ አድርጐ ይናገራል:: አት : “አታልሎህ በእኔ ፈንታ እርሱን እንዲትመርቅ አድረጐሃል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)::

ለእኔ ያስቀረኼው ምንም ምርቃት የለም?

ያዕቆብን የባረከውን ዓይነት በረከት አባቱ እንደማይባርከው ዔሣው ያውቃል ይስሐቅ ያዕቆብን በሚባርክበት ጊዜ ሳይናገር የቀረው ካለ ዔሣው ይጠይቀዋል

ልጄ ለአንተ ምን ላደርግልህ እችላለሁ?

ይስሐቅ ጥያቄ በመጠቀም ምንም ሊያደርገው የሚችለው ነገር እንደሌለ በአጽንዖት ይናገራል:: አት “ለአንተ የማደርገው የቀረ ነገር የለም” (ቅኔ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

Genesis 27:38

አባቴ ሆይ በረከትህ አንዲት ብቻ ናትን?

ይህ በአዎንታዊ መንገድ ሊነገር ይችላል:: አባቴ ሆይ አንድ የቀረ መረከት ለእኔ የሚሆን አለህን?

Genesis 27:39

እርሱን አለው

ዔሣውን አለው

ቦታውን ተመልከት

ትኩረት አድርግ ስለቦታው የሚናገረው እውነትና ጠቃሚ ነው

ከምድር በረከት የራቀ

ይህ ስለምድር ለምነት የሚናገር ምሳለያዊ አነጋገር ነው አት ለም ያልሆነ መሬት

ለአንተ…. አንተ

በ27:39-4ዐ እነዚህ ተውላጤ ስሞች ነጠላና ዔሣውን ያመለክታሉ:: ነገር ግን ይስሐቅ የሚናገረው ለዔሣው ትውልድም የሚሆን ነው:: ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ::

ከላይም ከሰማይ ጠል

ጠል በሌሊት በተክሎች ላይ የሚሆን የውሃ ጠብታ ነው:: በትርጉም ይህን ግልጽ ማድረግ ይቻላል:: አት: “ተክሎችዎን ለማጠጣት የሌሊት ጠል” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በሰይፍ ትኖራለህ

ሰይፍ ለአመጽ የሚቆም ነው:: አት: “ለመኖር የሚያስፈልግህን ለማግኘት ሰዎችን ትዘርፋለህ ትገድላለህ” (ተዛማጅ ተመሣሣይ ምትክ ቃል ስለመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ቀንበሩ ከጫንቃህ ላይ ወዲያው ትጥላለህ

ይህ አንድ ጌታ እንዳለውና የጌታውም የበላይ አገዛዝ አንደሚሸከምበት ቀንበር እንደተጫነበት ተደርጐ ተነግሮአል አት ከግዛቱ ራስህን ነጻ ታወጣለህ:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 27:41

ዔሣውም በልቡ እንዲህ ብሎ አሰበ

“ልብ” ራሱ ዔሣውን ያመለክታል:: አት: “ዔሣው ለራሱ እንዲህ አለ” (ተዛማጅ ተመሣሣይ ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ) የአባቴ የለቅሶ ቀን ቀርቦአልና ይህ የቤተሰብ አባል ሲሞት አንድ ሰው የሚያዝንበት ቀናት ያመለክታል

የታላቅ ልጇ የኤሣው ሀሳብ ለርብቃ ተረገራት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “አንድ ሰው የዔሣውን ዕቅድ ለርብቃ ነገራት“ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እይ

“ተመልከት” “አዳምጥ” “ለምናገረው ነገር ትኩረት ስጥ”

ራሱን እያረጋጋ ነው

ራሱን ጥሩ ስሜት እንዲሰማው እያደረገ ነው

Genesis 27:43

አሁንም

ይህ “አሁን ጊዜ” ማለት አይደለም:: ነገር ግን የሚቀጥለው አስፈላጊ ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ተጠቅሞአል::

ወደ ላባን ቶሎ ሽሽ

ቶሎ ከዚህ ሽሽ እናም ወደ ላባን ሂድ

ለጊዜ

ለተወሰነ ጊዜ

የወንድምህ ቁጣ እስኪበርድ

ወንድምህ እስኪበርድ

የወንድምህ ቁጣ ከአንተ እስኪመለስ

ያለ መቆጣት ቁጣ ከአንድ ሰው ወደ ሌላ አቅጣጫ እንደሚዞር ተደርጐ ተነግሮአል:: አት: “በአንተ ላይ መቆጣቱን እስኪተው ድረስ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሁለታችሁን በአንድ ቀን ለምን ሊጣ?

ርብቃ ሥጋትዋን ለመግለጽ ጥያቄ ትጠቀማለች አት ሁለታችሁን በአንድ ቀን ማጣት አልፈልግም! (ቅኔ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ሁለታችሁን በአንድ ቀን አጣለሁ

ይህ የሚገልጸው ኤሣው ያዕቆብን ከገደለ እርሱ ደግሞ ገዳይ በመሆኑ ስለሚገድሉት ነው:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አጣለሁ

ልጆቹዋ እንደሚሞቱባት የሚያመላክት ለዛ ያለ አገላለጽ ነው (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ አንድን ነገር የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 27:46

መኖር አስጠልቶኛል

ኤሣው የኬጢያውያን ሴት በማግባቱ ርብቃ መንኛ እንደተናደደች በማግነን ትኩረት መስጠትዋ ነው:: አት: “በማምረር ጠልቸዋለሁ” (hyperbole and Generalization/

የኬጢያውያን ሴት ልጆች

“እነዚህ የኬጢያውያን ሴቶች” ወይም “የኬጢያውያን ትውልጆች”

እንደነዚህ ሴቶች ከዚህ አገር ሴቶች ልጆች

“የአገሩ ሴቶች ልጆች” የአገሩ ሴቶች ማለት ነው:: አት: “በአገሩ የሚኖሩ እንደ እነዚህ ሴቶች” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይጠቀሙ)

በሕይወት መኖር ለምኔ ነው?

ያዕቆብ ከኬጢያውያን ሴት ልጆች የሚያገባ ከሆነ ርብቃን ማነኛ እንደሚያስከፋት በማግነን ጥያቄ ትጠቀማለች:: አት: “ሕይወቴ የከፋ ይሆናል”


Chapter 28

1 ይስሐቅ ያዕቆብን ጠርቶ መረቀው፤ እንዲህም ሲል አዘዘው፣ "ከነዓናዊት ሴት እንድታገባ፤ 2 ይልቅስ ተነሥተህ በመስጴጦምያ ወዳለው ወደ እናትህ አባት ወደ ባቱኤል ቤት ሂድ፤ እዚያም ከአጎትህ ከገባ ሴቶች ልጆች አንዷን አግባ፤ 3 ሁሉን የሚችል እግዚአብሔር ይባርክህ፤ ብዙ ልጆችም ይስጥህ፤ የብዙ ሕዝቦችም አባት ያድርግህ፤ 4 አብርሃምን እንደባረከ አንተንና ዘርህን ይባርክ፤ ይህንንም ለአብርሃም ሰጥቶት የነበረውንና አንተም ደስተኛ ሆነህ የኖርክበት ምድር ርስት አድርጎ ይስጥህ።" 5 በዚህ ሁኔታ ይስሐቅ ያዕቆብን አሰናበተው፤ ያዕቆብም በመስጴጦምያ ወደሚያኖረው ወደ ላባ ሄደ፤ ላባ የያዕቆብና የዔሳው እናት የርብቃ ወንድም ነበረ፤ አባቱም ሶርያዊው ባቱኤል 6 ይስሐቅ ያዕቆብን እንደመረቀና ሚስት እንደሚፈልግ ወደ መስጴጦምያ እንደላከው ዔሳው ተረዳ፤ ይስሐቅ ያዕቆብን ሲመርቀው "ከነዓናዊት ሴት እንዳታገባ" ብሎ ያዘዘው መሆኑንም ሰማ፤ 7 ያዕቆብ ለአባቱና ለእናቱ በመታዘዝ ወደ መስጴቶምያ መሄዱንም ተረዳ፤ 8 በዚህም አባቱ ይስሐቅ የከነዓንያውያንን ሴቶች እንደማይወድ ዔሳው ተገነዘበ፤ 9 ስለዚህ ከዚህ በፊት ከገባቸው ሌላ በተጨማሪ ወደ አብርሃም ልጅ ወደ እስማኤል ሄዶ ልጁን ማሕላትን አገባ፤ እርስዋም የነባዮት እኅት ናት። 10 ያዕቆብ ቤርሳቤህን ትቶ ወደ ካራን ለመሄድ ተነሣ፤ 11 ፀሐይ በጠለቀች ጊዜ ወደ አንድ ስፍራ መጥቶ ዐፈር፤ በዚያም አንድ ድንጋይ ተንተርሶ ተኛ፤ 12 በሕልሙም ከመሬት እስከ ሰማይ የሚደርሰው መሰላል አየ፤ በመሰላሉም የእግዚአብሔር መላእክት ወደ ላይ ይውጡና ወደ ታች ይውረዱ ነበር። 13 እግዚአብሔር በአጠገቡ ቆሞ እንዲህ አለው፣ "እኔ የአባትህ የአብርሃምና የይስሐቅ አምላክ እግዚአብሔር ነኝ፤ ለአንተና ለዝርያዎችህ እንዲሆን ይህን የተገኘበት ምድር እሰጥሃለሁ። 14 ዘርህን እንደ ምድር አሸዋ አበዛዋለሁ፤ እነርሱ በሁሉ አቅጣጫ ይዞታቸውን ያስፋፋሉ፤ በአንተና በዘርህ የዓለም ሕዝቦች ሁሉ ይባረካሉ። 15 አይዞህ! እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፤ በምትሄድበት ስፍራ ሁሉ እጠብቅሃለሁ፤ ወደዚያም ምድር በደህና እመልስሃለሁ፤ የገባሁልህን ቃል ኪዳን ሁሉ እፈፅምልሃለሁ፤ ከቶም አልተውህም።" 16 ያዕቆብም ከእንቅልፉ ነቃና "በእርግጥ እግዚአብሔር በዚህ ስፍራ አለ፤ እኔ ግን ይህን አላወቅሁም ነበር"አለ። 17 በጣም ፈርቶም ስለነበር "ይህ እንዴት የሚያስፈራ ቦታ ነው፤ ይህ የእግዚአብሔር ቤት መሆን አለበት፤ ወደ ሰማይ የሚያስገባው በር ይህ ነው"አለ። 18 ያዕቆብ በማግሥቱም ጠዋት በማለዳ ተነሣ፤ ተንተርሶት የነበረውንም ድንጋይ መታሰቢያ እንዲሆን እንደ ሐውልት አቆመው፤በላዩ ላይም የወይራ ዘይት አፈሰሰበት። 19 ይህንንም ስፍራ "ቤትኤል"ብሎ ሰየመው፤ ይህ ስፍራ ከዚያ በኋላ ሎዛ እየተባለ ይጠራ ነበር። 20 ከዚህ በኋላ ያዕቆብ እንዲህ ብሎ ለእግዚአብሔር ተሳለ "ከእኔ ጋር ሆነህ በምትሄድበት መንገድ ብትጠብቀኝ፣ የሚያስፈልገኝን ምግብና ልብስ ብትሰጠኝ፣ 21 ወደ አባቴም ቤት በሰላም ብትመልሰኝ፤ አንተ አምላኬ ትሆናለህ፤ 22 ይህ ለመታሰቢያነት ያቆምሁት ድንጋይ ወደ ፊት የእግዚአብሔር ቤት ይሆናል፤ ከምትሰጠኝም ሁሉ ከዐሥር አንዱን እጅ ለአንተ እሰጣለሁ።"



Genesis 28:1

አታግቡ

አታግባ

ተነሣ ሂድ

ወዲያውኑ ሂድ

ጳዳን አራም

ይህ የመስጴጦምያ ግዛት ሌላ ስሙ ሲሆን የአሁኑ ራቅ የሚገኝበት ቦታ ነው:: በዘፍጥረት 25:2ዐ ይህ እንዴት አንደተተረጐመ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

ቤት

የሰውየው ትውልድ ወይም ሌሎች ዘመዶች: አት: “ቤተሰብ” (ተዛማጅ ተመሣሣይ ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ባቱኤል

ባቱኤል የርብቃ አባት ነው በዘፍጥረት 22፡22 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

የእናትህ አባት

ወንድ አያትህ

ሴት ልጆች መካከል

ከሴት ልጆች

የእናትህ ወንድም

አጐትህ

Genesis 28:3

አጠቃላይ መረጃ

ይስሐቅ ለያዕቆብ መናገሩን ቀጠለ

ልጆች አፍራ ዘርህን ያብዛው

ያብዛው የሚለው ቃል እግዚአብሔር ያዕቆብን እንዴት ፍሬያማ እንደሚያደርገው ይገልጻል:: አት: “ብዙ ልጆችንና ትውልድ ይሰጥሃል” (ድርብ ቃላት ይመልከቱ)

ለአብርሃም የሰጠውን በረከት ለአንተና ለዘሪህ ይስጥ

ይህ የሚናገረው አንድን ሰው ስለመባረክ ሲሆን በረከት አንድ ሰው ሊሰጥ እንደሚችል ዕቃ ተደርጐ ተገልጾአል ረቂቅ ስም “በረከት” “ይባርክ” በሚለው ሊገለጽ ይችላል:: አት: “አብርሃምን እንደባረከ አንተንና ዘርህን እግዚአብሔር ይባርክ” ወይም “ለአብርሃም የገባውን ተስፋ ለአንተና ለዘርህ እግዚአብሔር ይስጥ”:: (ዜይቤያዊ አነጋገርና ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

ምድሪቱን ያወርስህ ዘንድ

እግዚአብሔር የከነዓንን ምድር ለያዕቆብና ለዘሩ መስጠቱ ልጅ ከአባቱ ገንዘብ ወይም ሀብት እንደሚወርስ ተደርጐ ተገልጾአል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የሚትኖርበትን ይህችን ምድር

“እስከአሁን ያለህበትን ምድር”

እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠውን

እግዚአብሔር ለአብርሃም ተሰፋ የሰጠውን

Genesis 28:5

ጳዳን አራም

ይህ የመስጴጦምያ ግዛት ሌላ ስሙ ሲሆን የአሁኑ ራቅ የሚገኝበት ቦታ ነው:: በዘፍጥረት 25:2ዐ ይህ እንዴት አንደተተረጐመ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

ባቱኤል

ባቱኤል የርብቃ አባት ነው በዘፍጥረት 22፡22 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

Genesis 28:6

አጠቃላይ መረጃ

ታሪኩ ከያዕቆብ ወደ ዔሣው ይዞራል

አሁንም

ይህ ቃል እዚህ የተጠቀመው ከተነገረው ታሪክ ወደ ዔሣው የሕይወት መረጃ ፍሰቱ መቀየሩን ለማመልከት ነው (ታሪካዊ ዳራ መረጃ ይመልከቱ)

ጳዳን አራም

ይህ የመስጴጦምያ ግዛት ሌላ ስሙ ሲሆን የአሁኑ ራቅ የሚገኝበት ቦታ ነው:: በዘፍጥረት 25:2ዐ ይህ እንዴት አንደተተረጐመ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

ሚስት ያግባ

ሚስትን ያግባ

እንዲሁም ደግሞ ይስሐቅም እንደባረከው አየ

እንዲሁም ይስሐቅ ያዕቆብን እንደባረከው ኤሣው አየ

የከነዓን ሴቶች

የከነዓን ሴት ልጆች ወይም የከነዓናዊያን ሴቶች

Genesis 28:8

አጠቃላይ መረጃ

የዔሣውን ታሪካዊ ዳራ ይቀጥላል

ዔሣው አየ

ዔሣው ተገነዘበ

ከነዓናውያን ሴቶች በአባቱ በይስሐቅ ዘንድ ተጠልተዋል

አባቱ ይስሐቅ የከነዓናውያንን ሴቶች አልተቀበለም

የከነዓን ሴቶች

የከነዓን ሴት ልጆች ወይም የከነዓናዉያን ሴቶች

ስለዚህም ሄዴ

በዚህ ምክንያት ሄዴ

በሚስቶቹ ተጨማሪ

ከነበሩ ሚስቶች ተጨማሪ

ማዕሌት

የእስማኤል ሴት ልጆች አንዷ ነች (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ነባዮት

ከእስማኤል ወንድ ልጆች አንዱ ነው (ስምችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 28:10

አጠቃላይ መረጃ

ታሪኩ እንደገና ወደ ያዕቆብ ይመለሳል

ወደ አንድ ሥፍራም ደረሰ ጸሐይም ጠልቃ ነበርና ከዚያ አደረ

ወደ አንድ ሥፍራ ደረሰ ጸሐይም ጠልታ ስለነበር አዳሩን ከዚያ ለማድረግ ወሰነ

Genesis 28:12

እርሱም ሕልም ዐለመ

ያዕቆብ ሕልም ዐለመ

በምድር ላይ ቆሞ

ታችኛው አካል መሬትን በነካ መንገድ ቆሞ

ጫፉ ሰማይ የሚደርስ

ይህ እግዚአብሔር የሚኖርበትን ቦታ ያመለክታል

እነሆም

እነሆም የሚለው ቃል ለሚቀጥለው አስደናዊ መረጃ ትኩረት ለመስጠት ነው

እግዚአብሔር በጫፉ ላይ ቆሞ

ተገቢ ትርጉሞች 1 እግዚአብሔር በመሰላሉ ጫፍ ላይ ቆሞ 2 እግዚአብሔር በያዕቆብ ጐን ቆሞ

ለአብርሃም ለአባትህ

እዚህ “አባት” ቅድመ ዘር ማለት ነው:: አት: “አብርሃም ለዘርህ” ወይም “አብርሃም ለቅድመ አያትህ”

Genesis 28:14

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ለያዕቆብ በሕልም መናገሩን ቀጠለ

ዘርህ እንደምድር አሸዋ ይሆናል

በቁጥር መብዛትን አግንኖ ለማሳየት እግዚአብሔር የያዕቆብን ዘር ከምድር አሸዋ ጋር ያነጻጽራል:: አት: “መቁጠር ከምትችሉት በላይ ብዙ ዘር ይሆንላችኋል” ተመሣሣይ አባባል/simile ይመልከቱ

እስከ ምዕራብ ትስፋፋለህ

ትስፋፋለህ በነጠላ የተቀመጠና ያዕቆብን ያመለክታል እዚህ ያዕቆብ ዘሩን ይወክላል:: አት: “መቁጠር ከሚትችለው በላይ ብዙ ዘር ይሆንልሃል” (ተዛማጅ ተመሣሣይ ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ትስፋፋለህ

ይህም ሕዝቡ የምድራቸውን ድንበር የሰፋሉ እናም ብዙ ምድር ይወርሳሉ ማለት ነው

ወደ ምዕራብ ወደ ምሥራቅ ወደ ሰሜን ወደ ደቡብ

እንዚህ ሀረጐች በጣምራ “ወደ ሁሉም አቅጣጫዎች” የሚል ትርጉም ለመስጠት ተጠቅመዋል:: (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

የምድርም ሕዝቦች ሁሉ በአንተና በዘርህ አማካይነት ይባረካሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “በአንተና በዘርህ በምድር ያሉ ሕዝቦችን እባርካለሁ” (ተሻጋረ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተነገር ይመልከቱ)

እነሆ እኔ

ትኩረት ስጥ እኔ የሚናገረው እውነትና ጠቃሚ ነው፤ እኔ

አልተውህም ሁሉንም እፈጽምልሃለሁ

ሁሉንም እስከሚፈጽምልህ ድረስ አልተውህም

እጠብቅሃለሁ

“ደኀንነትህን እጠብቃለሁ” ወይም “እከላከልልሃለሁ”

እንደገና ወደዚችም ምድር እመልስሃለሁ

ወደዚህች ምድር እመልስሃለሁ

Genesis 28:16

ከእንቅልፉ ሲነሣ

ከእንቅልፉ ሲነቃ

የእግዚአብሔር ቤት … የሰማይ ደጅ

የሰማይ ደጅ የሚለው ሀረግ የሚገልጸው የእግዚአብሔር ቤት እና የእግዚአብሔር መኖሪያ መግቢያ ቦታ እንደሆነ ነው (ድርብ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

ይህ የሰማይ ደጅ ነው

ይህ ስለ እግዚአብሔር መኖሪያ ቦታ መግቢያ የሚናገረው በአካል እንደሚታይ አንድ ሰው በር ከፍቶ ሰዎችን እንደሚያስገባው የመንግሥት ቤት ተደረጐ ተገልጾአል:: (ዘይቤያዊ አባባል ይመልቱ)

Genesis 28:18

ሐውልት

ትልቅ ድንጋይ ወይም በጫፉ ቅርጽ ያለበት ለማስታወሻነት የቆመ ሐውልት ነው

በላዩ ላይ የወይራ ዘይት አፈሰሰበት

ያዕቆብ ሐውልቱን ለእግዚአብሔር መቀደሱን የሚያመለክት ድርጊት ነው:: የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “ሐውልቱን ለእግዚአብሔር ለመቀደስ ዘይት በላዩ ላይ አፈሰሰበት” (ምልክታዊ ድርጊት ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ቤተል

ቤተል ማለት የእግዚአብሔር ቤት የሚለውን ተረጓሚዎች እንደ ግርጌ ማስታወሻ ያስቀምጣሉ

ሎዛ

ይህ የከተማይቱ ስም ነው

Genesis 28:20

ስእለት ተሳለ

“ስእለት አደረገ” ወይም “በተለይ ለእግዚአብሔር ቃል ገባ”

እግዚአብሔር እንዲህ…. እግዚአብሔር አምላኬ ይሆናል

ያዕቆብ እግዚአብሔርን በሶስተኛ ሰው አገላለጽ ያናግረዋል ይህ በሁለተኛ ሰው አገላለጽ ሊገለጽ ይችላል:: አት: አንተ እንዲህ…የማመልከው አምላኬ ትሆናለህ” (ተዛማጅና ተመሣሣይ ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

የሚበላውን እንጀራ ቢትሰጠኝ

እዚህ “እንጀራ” አጠቃላይ ምግብ ይገልጻል (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ወደ አባቴ ቤት

“ቤት” ለያዕቆብ ቤተሰብን ይገልጻል አት ወደ አባቴና ወደሌሎች የቤተሰብ አባላት (ተዛማጅና ተመሣሣይ ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

የተቀደሰ ድንጋይ

ድንጋዩ እግዚአብሔር የተገለጠበትን ቦታ ያመለክታልና ሰዎች እግዚአብሔርን የሚያመልኩበት ቦታ ይሆናል


Chapter 29

1 ያዕቆብ ጉዞውን ቀጥሎ በስተ ምሥራቅ ወዳለው አገር ደረሰ፤ 2 እዚያም በሜዳ ላይ አንድ የውሃ ጉድጓድ አየ፤ በሦስት የተከፈሉ የበግ መንጋዎች በጉድጓድ ዙሪያ ነበሩ፤ መንጋዎቹ ውሃ የሚጠጡት ከዚሁ ጉድጓድ ነበር፤ ጉድጓዱም የሚዘጋበት ድንጋይ ትልቅ ነበር፤ 3 መንጋዎቹ ሁሉ እዚያ ከተሰበሰቡ በኋላ እረኞቹ ድንጋዩን አንከባለው ከጉድጓዱ ውሃ ያጠቱአቸው ነበር፤ መንጋዎቻቸውን ካጠጡ በኋላ ግን ድንጋዩንም መልሰው በጉድጓዱ አፍ ላይ ይከዱኑታል። 4 ያዕቆብም እረኞቹን "ወዳጆቼ ሆይ! ከየት ነው የመጣችሁት?" ብሎ ጠየቃቸው። እነሱም "እኛ የመጣነው ከካራን ነው" አሉት። 5 እርሱም "የናኮርን የልጅ ልጅ ላባን ታውቁታላችሁን?" ብሎ ጠየቃቸው። እነሱም "አዎ እናውቀዋለን" አሉት። 6 እርሱም "ለመሆኑ እርሱ ደኅና ነውን?" አላቸው። እነርሱም "አዎ፣ ደኅና ነው፤ እንዲያውም ልጁ ራሔል ያችውልህ! በጎች እየነዳች በመምጣት ላይ ነች" አሉት። 7 ያዕቆብም "ጊዜው ገና ቀን ነው፤ መንጋዎቻቸውንም ወደ ቤት የምታስገቡበት ሰዓት ገና አልደረሰም፤ ታዲያ ለምን ውሃ አጠጥታችሁ አታሰማሩአቸውም? ፤ አለ። 8 እነርሱም "እረኞች ሁሉ መንጋዎቻቸውን ይዘው እዚህ ከመሰብሰባቸው በፊት ምንም ማድረግ አንችልም፤ ሁሉም እዚህ ከመጡ በኋላ ግን ድንጋዩን በኅብረት አንከባለን በጎቹን እናጠጣቸዋለን" አሉት። 9 ያዕቆብም ከእረኞቹ ጋር በመነጋገር ላይ ሳለ ራሔል የአባትዋን በጎች ይዛ ወደዚያ መጣች፤ ምክንያቱም እርስዋ የበጎች እረኛ ነበረች። 10 ያዕቆብ ያጉቱን የላባን በጎች እየነዳች ስትመጣ ራሔልን አይቶ ወደ ጉድጓድ ሄደ፤ ጉድጓዱ የተከደነበትንም ድንጋይ አንከባሎ በጎቹን አጠጣቸው። 11 ከዚያ በኋላ ራሔልን ሳማት። ከደስታውም ብዛት የተነሣ አለቀሰ፤ 12 "እኔ የአባትሽ እኅት የሆነችው የርብቃ ልጅ ሄደች። 13 ላባም የእኅቱ ልጅ ያዕቆብ መምጣቱን በሰማ ጊዜ ሊቀበለው ፈጥኖ ሄደ፤ አቅፎ ከሳመውም በኋላ ወደ ቤት አመጣው፤ ያዕቆብ የሆነውን ሁሉ ለላባ ነገረው፤ 14 ላባም "በእርግጥ አንተ ቅርብ የሥጋ ዘመዴ ነህ" አለው፤ ያዕቆብም አንድ ወር ያህል ከአጎቱ ጋር ተቀመጠ። 15 ላባ ያዕቆብን "ዘመዴ በመሆንህ ብቻ በነፃ ልታገለግለኝ አይገባህም፤ ስለዚህ ምን ያህል ደመወዝ ላስብልህ? አለው። 16 ላባ ሁለት ሴቶች ልጆች ነበሩት፤ ታላቂቱ ልያ፤ ታናሽቱ ራሔል ይባሉ ነበር። 17 ልያ ዐይነ ልም ስትሆን፣ ራሔል ግን ቁመናዋ የሚያምር የደስ ደስ ያላት ነበረች። 18 ያዕቆብ ራሔልን እጅግ ስለወደዳት "ራሔልን ብትድርልኝ ሰባት ዓመት አገለግልሃለሁ" አለ። 19 ላባም "ለሌላ ሰው ከምሰጣት ይልቅ ለአንተ ብሰጥህ ይሻለኛል፤ እሺ ተስማምቼአለሁ፤ እዚሁ ከእኔ ጋር ኑር" አለው። 20 ያዕቆብ ራሔልን ለማግባት ሰባት ዓመት አገለገለ፤ ይሁን እንጂ ራሔልን በጣም ይወዳት ስለነበር የቆየበት ጊዜ ጥቂት ቀን ብቻ መስሎ ታየው። 21 ከዚያ በኋላ ያዕቆብ ላባን "እነሆ የአገልግሎት ዘመኔ ተፈፅሞአል፤ ሚስት እንድትሆነኝ ልጅህን ስጠኝ" አለው። 22 ላባም የሠርግ ድግስ አዘጋጅቶ በአቅራቢያው የሚገኙትን ሰዎች ሁሉ ጠራ። 23 ነገር ግን ላባ በራሔል ምትክ ልያን ለያዕቆብ ሰጠው፤ ያዕቆብም ከልያ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት አደረገ። 24 ላባ ሴት አገልጋዩን ዚልፋን አገልጋያዋን እንድትሆን ለልጁ ለልያ ሰጣት። 25 በማግስቱ ጠዋት ያዕቆብ አብራው ያደረችው ልያ መሆንዋን ባወቀ ጊዜ ወደ ላባ ሄዶ "ይህ ያደረግህብኝ ነገር ምንድን ነው? ያገለገልሁህ ራሔልን ለማግኘት አልነበረም? ታዲያ ለምን አታለልከኝ"አለው። 26 ላባም "ታላቂቱ ሳትዳር፤ ታናሺቱን መዳር የአገራችን ልማድ አይደለም፤ 27 የልያ ሠርግ ሰባት ቀን እስኪሞላው ድረስ ጠብቅ፤ ከእንግዲህ ወዲይ ሰባት ዓመት የምታገለግለኝ ከሆነ ራሔልን እሰጥሃለሁ" አለው። 28 ያዕቆብም ነገሩ ተስማማ፤ ከልያ ጋር ሰባት ቀን ተሞሽሮ ከቆየ በኋላ፤ ላባ ልጁን ራሔልን ለያዕቆብ ሳረለት። 29 ላባ ሴት አገልጋዩን ባላን አገልጋይዋ እንድትሆን ለልጁ ለራሔል ሰጣት። 30 ያዕቆብ ከራሔልም ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት አደረገ፤ ከልያም አብልጦ ወደዳት፤ ከዚያ በኋላ ላባን ሰባት ዓመት አገለገለው። 31 ልያ የራሔልን ያህል እንዳልተወደደች እግዚአብሔር ባየ ጊዜ መውለድ እንድትችል ማሕፀንዋን ከፈተላት፤ ራሔል ግን መኻን ሆነች፤ 32 ልያ ርርግዛ ወንድ ልጅ ወለደች፤ "እግዚአብሔር መከራዬን ተመለከተ፤ ከእንግዲህስ ወዲያ ባሌ ይወደኛል" ስትል ስሙን ሮቤል አለችው። 33 እንደገና አረገዘችና ሌላ ወንድ ልጅ ወደች፤ "እግዚአብሔር እንዳልተወደድሁ ሰማ፤ ይህንንም ልጅ ደግሞ ሰጠኝ' ስትል ስሙን ስምዖን አለችው። 34 እንደገና 'አረገዘችና ሌላ ወንድ ልጅ ወለደች፤ "እንግዲህ ሦስት ወንዶች ልጆች ስለ ወለድሁለት ባሌ ከእኔ ጋር በፍቅር ይጠመዳል" ስትል ስሙን ሌዊ አለችው፤ 35 እንደገና አረገዘችና ውንድ ልጅ ወለደች፤ "አሁንስ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ" ስትል ስሙን ይሁዳ አለችው፤ ከዚህ በኋላ መውለድ አቋረጠች።



Genesis 29:1

የምሥራቅ ሰዎች

ከከነዓን ምድር በስተምሥራቅ የሚገኙ የጳዳን አራም ሰዎች ማለት ነው::

እነሆ በአንድ ሜዳ ላይ ሶስት የበግ መንጋዎች ተኝተው በነበሩበት

እነሆ የሚለው ቃል በትልቁ ታሪክ ውስጥ አንድ ሌላ ክስተት መጀመሩን ያመለክታል:: በሚትተረጉሙበት ቋንቋ ይህን የመግለጽ መንገድ ሊኖሮት ይችላል::

ከዚያ ጉድጓድ

ከዚሁ ጉድጓድ ይህ ሀረግ ታሪኩን ወደ ዳራው መረጃ ይመልስና እንዴት እረኞች በጐችን ውሃ እንደሚያጠጡ ይናገራል

እነርሱ ውሃ ያጠጣሉ

“እረኞች ውሃ ያጠጣሉ” ወይም “በጐችን የሚጠብቁ ውሃ ያጠጣሉ”

የጉድጓዱ አፍ

አፍ ጉድጓዱ የተከፈተበትን ቦታ ያሳያል:: አት: “ጉድጓዱ የተከፈተበት ቦታ”

Genesis 29:4

ያዕቆብም እነርሱን አለ

ያዕቆብም እረኞቹን አለ

ወንድምቼ

ይህ ለእንግዶች በትህትና ሰላምታ የማቅረብ መንገድ ነው

የናኮር ወንድ ልጅ ላባ

አዚህ ወንድ ልጅ ወንድ ዘርን ያመለክታል ሌላ ተገቢ ትርጉም የናኮር የልጅ ልጅ ላባ

እነሆ ተመልከት ራሔል በጎችን እየነዳች በመምጣት ላይ ነች

አሁን ተመልከት የእርሱ ሴት ልጅ ራሔል ከበጎች ጋር በመምጣት ላይ ነች

Genesis 29:7

ገና ቀትር ነው

“ገና ጸሐይ በሰማይ ላይ ነች/ጊዜው ገና ነው” ወይም “ጸሐይ ገና በማብራት ላይ ነች”

መንጎች እስኪሰበሰቡ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “መንጐችን እስኪሰበስቡ” (ተሻጋረ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተነገር ይመልከቱ)

መሰብሰብ

ይህም ሌሊቱን እንዲያሳልፉ በቅጥር ውስጥ መሰብሰብ ማለት ነው:: የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀት እና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ወደ ግጦሽ ይመለሱ

በሜዳ ያለውን ሣር ይመገቡ

ውሃ ሊናጠጣቸው አንችልም

ውሃ ሊናጠጣቸው መጠበቅ አለብን ይህ ፈቃደኝነት ሳይሆን ጊዜን በሚመለከት ነው

መንጐቹ ሁሉ እስኪሰበሰቡ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ሌሎች እረኞች መንጐቻቸውን እስኪሰበስቡ” (ተሻጋረ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተነገር ይመልከቱ)

ከጉድጓዱ አፍ

እዚህ አፍ ጉድጓዱ የተከፈተውን ቀዳዳ ያመለክታል አት ከጉድጓዱ ወይም ጉድጓዱ በተከፈተበት (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 29:9

የእናቱ ወንድም

አጐቱ

የጉድጓዱ አፍ

እዚህ “አፍ” የተከፈተበትን ቦታ ያመለክታል:: አት: “ጉድጓዱ” ወይም “ጉድጓዱ የተከፈተበትን ቦታ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 29:11

ያዕቆብም ራሔልን ሳማት

በጥንታዊቷ ቅርብ ምሥራቅ በመሳም ሰላምታ መለዋወጥ የተለመደ ነው:: ነገር ግን በወንዶች ዘንድ እምብዛም የታወቀ ነው:: በሚትተረጉሙበት ቋንቋ ባህል እንዲህ ዓይነቱ ስሜትን በመግለጽ ዘመዳሞች ሰላምታ የመለዋዋጥ ነገር ካለ ይህን ይጠቀሙ:: ከሌለ ግን ሌላ ተገቢ አባባል ይጠቀሙ::

ድምጹን ከፍ አድርጐ አለቀሰ

ያዕቆብ የሚያለቅሰው ደስተኛ በመሆኑ ነው የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉሙ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የአባትዋ ዘመድ

ለአባትዋ የሚዛመድ

Genesis 29:13

የእርሱ እኀት ልጅ

የእኀቱ ልጅ

አቀፈው

አቀፈው

ሳመው

በጥንታዊቷ ቅርብ ምሥራቅ በመሳም ለዘመድ ሰላምታ ማቅረብ የተለመደ ነው:: ነገር ግን ይህ በወንዶች መካከል የታወቀ ነው:: በሚተረጉሙት ቋንቋ ለዘመድ የሚቀርብ ሰላምታ ስሜትን የሚገልጽ ከሆነ ይህን ይጠቀሙበት:: ካለሆነ ግን ሌላ ተገቢ አባባል ይጠቀሙ::

ያዕቆብም ሁኔታውን ሁሉ ለላባ ነገረው

“ከዚያም ያዕቆብ ለራሔል የነገረውን ሁሉ ለላባ ነገረው”

የአጥንቴ ፍላጭ የሥጋዬ ቁራጭ

እነዚህ ሀረጐች በቀጥታ የሚዛመዱ ናቸው:: አት: “የእኔ ዘመድ” ወይም “የቤተሰቤ አባል” (ተዛማጅ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 29:15

ዘመዴ በመሆንህ ብቻ በነጻ ሊታገለግለኝ አይገባምና…?

ስለሚሠራለት ሥራ ለያዕቆብ መክፈል ስለአለበት ላባን ይህንን አግንኖ ለመናገር ጥያቄ ይጠቀማል:: ይህ በአዎንታዊ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ዘመዴ ቢትሆንም ለሚትሠራልኝ መክፈል በእርግጥ ትክክል ነው” See:RhetoricalQuestionandLitotes

የልያ ዐይን ልም ነው

ተገቢ ትርጉሞች 1 የልያ ዓይኖች ልም ነበሩ 2 የልያ ዐይኖች ታማሚ ነበሩ

ያዕቆብ ራሔልን ወደደ

እዚህ ወደደ የሚለው ቃል በአንድ ወንድና ሴት መካከል የሚሆን ስሜታዊ ወዋደድን ያመለክታል

Genesis 29:19

ለሌላ ወንድ ከሚሰጣት ይልቅ

ለሌላ ወንድ ከሚድራት ይልቅ

እነዚያ ጥቂት ቀናት ብቻ ሆኖ ታየው

“ነገር ግን ጊዜው ጥቂት ቀናት ሆኖ ታየው”

ለእርስዋ ካለው ፍቅር

“ለእርስዋ ያለውን ፍቅር ስመዝን” ወይም “ለእርስዋ ካለው ፍቅር የተነሣ”

Genesis 29:21

እንዳገባት ዘንድ ሚስቴን ስጠኝ ቀኔ ተፈጽሞአልና

ቀኔ ተፈጽሞአል የሚለው ሀረግ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: ይህ emphatic ዐረፍተ ነገር ነው:: አት: “ለአንተ መሥራት የሚገባኝን ጊዜ ስለፈጸምሁ እንዳገባት ሚስቴን ስጠኝ” ወይም “ለሰባት ዓመታት ስላገለገልሁ እንዳገባት ራሔልን ስጠኝ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ሠርግ አዘጋጀ

የጋብቻ ሠርግ አዘጋጀ ምናልባት ላባን ሌሎች ሰዎች እንዲያዘጋጁ አደረገ:: አት: “ሌሎች የጋብቻ ሠርግ እንዲያዘጋጁ አደረገ”:: (ተዛማጅ ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤ ይመልከቱ)::

Genesis 29:23

አብሮአት ተኛ

ይህ የሚገልጸው ምሽት ስለነበረና ስላላያት ከልያ ጋር መሆኑን ያዕቆብ አላወቀም ነበር:: የዐረፍተ ነገሩ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ላባን ዘለፋ የተባለች አገልጋዩን ለልጁ ለልያ ደንገጡር እንድትሆን ሰጣት

እዚህ ጸሐፊው ላባን ዘለፋን ለልያ እንደሰጠ መረጃ ይሰጣል፡፡ ዘለፋን ለልያ ከሠርግ በፊት ሳይሰጣት አይቀርም:: (ታሪካዊ ዳራ መረጃ ይመልከቱ)

እነሆ ልያ ሆና ተገኘች

ያዕቆብም ልያ በአልጋ አብሮአት በማየቱ ተገረመ:: “እነሆ” የሚለው ቃል ያዕቆብ ባየው ነገር እንዴት እንደተደነቀ የሚያሳይ ነው፡፡

ምነው እንደዚህ አደረግህብኝ?

ያዕቆብ ቁጣውንና መገረሙን ለመግለጽ ጥያቄ ይጠቀማል ይህ ቅኔ አዘልጥያቄ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡ “ይህን ለእኔ ታደርጋለና ብዬ አላምንህም” (See: RhetoricalQuestion)

ያገለገልሁህ ለራሔል ብዬ አልነበረምን?

ያዕቆብ እነዚህን ጥያቄዎች የሚጠቀመው ላባን ያታለለውን ጉዳቱን ለመግለጽ ነው ይህ ቅኔ አዘል ጥያቄ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊገለጽ ይችላል ራሔልን ለማግባት ሰባት ዓመት አገልግየሃለሁ (See: Rhetorical Question)

Genesis 29:26

እንሰጥ ዘንድ ወግ አይደለም

በቤተሰባችን አንሰጥም

ለዚህች ሴት ልጅ ይህን የጫጉላ ሳምንት ፈጽም

የልያን ጫጉላ ሳምንት ፈጽም

ሌላኛይቱን ደግሞ እንሰጣለን

የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት በሚቀጥለው ሳምንት ደግሞ ራሔልን እንሰጥሃለን (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 29:28

ያዕቆብም እንዲሁ አደረገ እናም የልያን ሳምንት ፈጸመ

ያዕቆብ ላባን የጠየቀውን አደረገ እናም የልያን ጫጉላ ሳምንት ማክበርን ፈጸመ

ባላ

ይህ የራሔል ሴት አገልጋይ ስም ነው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ያዕቆብም ከራሔል ጋር ተኛ

ጋብቻዊ ግንኙነት እንደፈጸሙ የሚገልጽ አክብሮታዊ ወይም ለዛ አባባል ነው

ራሔልን ወደዳት

በአንድ ወንድና በአንድ ሴት መካከል የሚሆን ስሜታዊ ፍቅር ያመለክታል

Genesis 29:31

ልያ አልተወደደችም

ይህ ተሻሪ ግሥ በያዘ መልክ ወይም በገቢር ዐረፍተ ነገር ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ያዕቆብ ልያን አልወደዳትም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እንዳልተወደደች

ያዕቆብ ራሔልን ከልያ ይልቅ እንደወደዳት በማተኮር አግንኖ የሚናገር ነው አት ከራሔል አሳንሶ ወደዳት (አግንኖና በገሃድ የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ማሕጸንዋን ከፈተላት

እግዚአብሔር ልያ እንዲትጸንስ ማድረጉ እግዚአብሔር ማሕጸንዋን እንደከፈተ ተደርጐ ተነግሮአል:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

መካን ነበረች

ሊትጸንስ አልቻለችም

ልያ ጸነሰች ልጅም ወለደች

ልያ ጸነሰች ወንድ ልጅም ወለደች

ስሙን ሮበል አለችው

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: ሮበል የሚለው ስም ‘ወንድ ልጅ አየሁ’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

እግዚአብሔር መከራዬን ስለተመለከተልኝ

ልያ ያዕቆብ ስላልተቀበላት በስሜታዊ ሕመም ነበራት:: “መከራ” የሚለው ረቂቅ ስም እንደ ግሥ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “እግዚአብሔር እንደተሰቃየሁ አየኝ” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

Genesis 29:33

እንደገናም ጸነሰች

እንደገናም ልያ ጸነሰች

ልጅ ወለደች

ወንድ ልጅ ወለደች

ስሙን ስምዖን ብላ ጠራችው

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ስምዖን የሚለው ስም ‘ተሰማ’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ባሌ ያቀርበኛል

ባሌ ያቅፈኛል

ሶስት ወንዶች ልጆች ስለወለድሁለት

ለእርሱ ሶስት ወንጆ ልጆች ወለድሁለት

ስው ሌዊ ይባላል

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ሌዊ የሚለው ስም ‘የተጠጋ’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 29:35

እንደገናም ጸነሰች

ልያ እንደገና አረገዘች

ወንድ ልጅ ወለደች

ወንድ ልጅን ወለደች

ስሙንም ይሁዳ ብላ ጠራችው

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ይሁዳ የሚለው ስም ‘ምሥጋና’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)


Chapter 30

1 ራሔል ለያዕቆብ አንድም ልጅ እንዳልወለደችለት ባየች ጊዜ በእኅቷ ቀናች። ያዕቆብንም፣ “ልጅ ስጠኝ አለበለዚያ እሞታለሁ” አለችው። 2 ያዕቆብም ራሔልን ተቆጥቶ፤ “እኔ የሆድሽን ፍሬ በነሳሽ በእግዚአብሔር ቦታ ነኝን?” አላት። 3 እርሷም፣ “እነሆ፣ አገልጋዬ ባላ አለችልህ፣ ልጆች እንድትወልድልኝና እኔም ደግሞ በእርሷ አማካይነት ልጆች እንዳገኝ ከእርሷ ጋር ተኛ” አለችው። 4 ስለዚህ ባላን እንደሚስት አድርጋ ሰጠችው፤ ያዕቆብም ከእርሷ ጋር የግብረ-ሥጋ ግንኙነት አደረገ። 5 ባላም አረገዘችና ወንድ ልጅ ወለደችለት። 6 ራሔልም፦ “እግዚአብሔር ፈረደልኝ፣ ልመናዬንም ሰምቶ ወንድ ልጅ ሰጥቶኛል” አለች። ስለዚህ ስሙን ዳን ብላ ጠራችው። 7 የራሔል አገልጋይ ባላ ዳግመኛ አረገዘችና ለያዕቆብ ሁለተኛ ወንድ ልጅ ወለደች። 8 ከእኅቴ ጋር ብርቱ ትግል ታግዬ አሸነፍኋት” አለች። ስለዚህ ስሙን ንፍታሌም ብላ ጠራችው። 9 ልያም ልጅ መውለድ ማቆሟን እንደተረዳች፣ አገልጋይዋን ዘለፋን ሚስት እንድትሆነው ለያዕቆብ ሰጠችው። 10 የልያ አገልጋይ ዘለፋም ለያዕቆብ ወንድ ልጅ ወለደችለት፣ 11 ልያም፣ “እንዴት የታደልሁ ነኝ!” ስትል ስሙን ጋድ ብላ ጠራችው። 12 የልያም አገልጋይ ዘለፋ ለያዕቆብ ሁለተኛ ልጅ ወለደችለት፤ 13 ልያም፣ “እጅግ ደስ ብሎኛል፣ ከእንግዲህ ወዲያ ሴቶች ‘ደስተኛዋ’ ይሉኛል አለች፤ ስሙንም ‘አሴር’ ብላ ጠራችው። 14 በስንዴ መከር ወራት ሮቤል ወደ ዱር ሄዶ እንኮይ አገኘ፤ ለእናቱ ለልያም አመጣላት፤ ራሔልም ልያን፣ “እባክሽን ልጅሽ ካመጣልሽ እንኮይ ስጪኝ” አለቻት። 15 ልያም፦ “ባሌን የቀማሽኝ አነሰና የልጄን እንኮይ ደግሞ ልትወስጂ አማረሽ?” አለቻት። ራሔልም፣ “ስለልጅሽ እንኮይ ዛሬ ያዕቆብ ከአንቺ ጋር ይደር” አለቻት። 16 በዚያ ምሽት ያዕቆብ ከእርሻ ሲመለስ፣ ልያ ወጥታ ተቀበለችውና፣ “በልጄ እንኮይ ስለተከራየሁህ የዛሬው አዳርህ ከእኔ ጋር ነው” አለችው። ያዕቆብም በዚያች ሌሊት ከእርሷ ጋር አደረ። 17 እግዚአብሔር የልያን ጸሎት ሰማ፣ ስለዚህ አረገዘችና ለያዕቆብ አምስተኛውን ወንድ ልጅ ወለደችለት። 18 ልያም፦ “አገልጋዬን ለባሌ በመስጠቴ እግዚአብሔር ደመወዜን ከፈለኝ” አለች። ስሙንም ይሳኮር አለችው። 19 ልያ አሁንም ደግማ ፀነሰች፤ ለያዕቆብም ስድስተኛውን ወንድ ልጅ ወለደች። 20 እርሷም፣ “እግዚአብሔር በከበረ ስጦታ አድሎኛል፣ ስድስት ወንዶች ልጆች ስለወለድሁለት ከእንግዲህ ባሌ አክብሮ ይይዘኛል” አለች፤ ስሙንም ዛብሎን አለችው። 21 ከዚያም በኋላ ሴት ልጅ ወለደች ስምዋንም ዲና አለቻት። 22 እግዚአብሔርም ራሔልን አሰበ፤ ጸሎትዋንም ሰምቶ ልጅ እንድትወልድ አደረጋት፤ 23 አርግዛም ወንድ ልጅ ወለደችና፣ “እግዚአብሔር ዕፍረቴን አስወገደልኝ” አለች፤ 24 ደግሞም ሌላ ወንድ ልጅ ይጨምርልኝ ስትል ስሙን ዮሴፍ ብላ ጠራችው። 25 ራሔል ዮሴፍን ከወለደች በኋላ ያዕቆብ ላባን እንዲህ አለው፦ “ወደ ተወለድሁበት አገር እንድመለስ አሰናብተኝ፤ 26 አንተን በማገልገል ያገኘኋቸውን ሚስቶቼንና ልጆቼን ስጠኝና ልሂድ፤ ምን ያህል አገልግሎት እንዳበረከትኩልህ ታውቃለህ።” 27 ላባም፣ “በአንተ ምክንያት እግዚአብሔር እንደባረከኝ በንግርት መረዳቴን ልነግርህ እወዳለሁ፤ 28 የምትፈልገውን ደመወዝ ንገረኝና እከፍልሃለሁ” አለው። 29 ያዕቆብም እንዲህ አለው፦ “እንዴት እንዳገለገልሁህና የከብትህም መንጋ በእኔ ጠባቂነት እንዴት እንደረባልህ አንተ ታውቃለህ፤ 30 እኔ ከመምጣቴ በፊት ጥቂት የነበሩት መንጋዎችህ አሁን እጅግ በዝተዋል፤ በተሰማራሁበት ሁሉ እግዚአብሔር በረከቱን አብዝቶልሃል። ታዲያ፣ ለራሴ ቤት የሚያስፈልገኝን የማቀርበው መቼ ነው?” 31 ላባም፣ “ታዲያ ምን ያህል ልክፈልህ?” ብሎ ጠየቀው። ያዕቆብም እንዲህ ሲል መለሰ፦ “እኔ የምልህን አንድ ነገር ብቻ ብታደርግልኝ መንጋህን ማሰማራቴንና መጠበቄን እቀጥላልሁ፤ 32 ዛሬ በመንጋዎችህ መካከል ልለፍና ዝንጉርጉርና ነቁጣ ጥቁርም የሆኑትን በጎች ሁሉ ልለይ፤ እንዲሁም ነቁጣና ዝንጉርጉር የሆኑትን ፍየሎች እመርጣለሁ፤ እነርሱም ደመወዜ ይሆናሉ፤ 33 ወደፊት ደመወዜን ለመቆጣጠር በምትመጣበት ጊዜ ታማኝነቴ ይታወቃል፤ ደመወዜን ለመቆጣጠር ስትመጣ ዝንጉርጉር ያልሆነ ወይም ነቁጣ የሌለበት ፍየል ብታገኝ፣ እንዲሁም ጥቁር ያልሆነ በግ ብታገኝ የተሰረቀ መሆኑን መረዳት ትችላልህ” አለው። 34 ላባም፣ “እሺ አንተ ባልከው እስማማለሁ” አለ። 35 ነገር ግን በዚያኑ ዕለት ከተባት ፍየሎች ሽመልመሌ የሆኑትን ወይም ነቁጣ ያለባቸውን ሁሉ እንዲሁም ከእንስት ፍየሎች ነቁጣ ያለባቸውን ዝንጉርጉር የሆኑትን ሁሉ መረጠ፤ ደግሞም ጥቋቁር የሆኑትንም በጎች ሁሉ ለየና ወንዶች ልጆቹን አስጠበቃቸው። 36 ከዚህ በኋላ ላባ መንጋውን ነድቶ የሦስት ቀን መንገድ ያህል ከያዕቆብ ርቆ ሄደ፤ ያዕቆብም የቀሩትን የላባን መንጋዎች መጠበቁን ቀጠለ። 37 ያዕቆብም ልብን፣ ለውዝና ኤርሞን ከሚባሉ ዛፎች እርጥብ በትሮችን ወሰደ፤ በበትሮቹ ያለው ነጭ እንዲታይ ሽመልመሌ አድርጎ ላጣቸው፤ 38 መንጋዎቹ ውሃ ለመጠጣት ሲመጡ ከፊት ለፊት እንዲያዩአቸው የተላጡትን በትሮች በውሃ ማጠጫዎቹ ውስጥ አደረጋቸው። መንጎቹም ስሜታቸው ሲነሣሣና ውሃ ለመጠጣት ሲመጡ፣ 39 በትሮቹን ፊት ለፊት እያዩ ይሳረሩ ነበር፤ ሽመልመሌ፣ ዝንጉርጉርና ነቁጣ የጣለባቸውንም ግልገሎች ወለዱ። 40 ያዕቆብ እነዚህን ግልገሎች ለብቻ ለየ፤ የቀሩትን ግን ዝንጉርጉርና ጥቁር በሆኑት በላባ መጋዎች ፊት ለፊት አቆማቸው፤ በዚህ ዓይነት የራሱን መንጋ ከላባ መንጋ ጋር ሳይቀላቅል ለብቻ አቆማቸው። 41 ያዕቆብም ብርቱ እንስቶች አውራ ፈልገው በሚቅበጠበጡበት ጊዜ በትሮቹ አቅራቢያ እንዲጠቁ በትሮቹን በውሃ ገንዳዎች ውስጥ ፊት ለፊታቸው ያስቀምጥ ነበር፤ 42 ደካማ በሆኑት እንስቶች ፊት ግን በትሮቹን አያስቀምጥም ነበር፤ ስለዚህ ደካሞቹ ለላባ ሲሆኑ፣ ብርቱዎቹ ለያዕቆብ ሆኑ። 43 በዚህም ሁኔታ ያዕቆብ እጅግ ባለጸጋ ሆነ፤ ብዙ መንጋዎች፤ ሴቶችና ወንዶች አገልጋዮች፣ ብዙ ግመሎችና አህዮችም ነበሩት።



Genesis 30:1

ራሔል ለያዕቆብ ልጅን እንዳልወለደች ባየች ጊዜ

ራሔል ማርገዝ እንዳልቻለች ባወቀች ጊዜ

እሞታለሁ

ራሔል ልጅ ባለመኖርዋ ምነኛ እንደተከፋች ማጋነንዋ ነው:: አት: ምንም እንደማልጠቅም ይሰማኛል:: (በማጋነንና በገሃድ የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ልጅ ስጠኝ

እንዳረግዝ አድርገኝ

ያዕቆብም ቁጣ በራሔል ላይ ነደደ

የያዕቆብ ቁጣ እንደ እሳት ተደርጐ ተገልጾአል፡፡ አት፡ “ያዕቆብ ራሔልን በጣም ተቆጣት” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እኔ እንዳትወልጂ ያደረግሽን እግዚአብሔርን መሰልኩሽን?

ይህ ያዕቆብ ራሔልን ለመቆጣት የተጠቀመው ቅኔያዊ ጥያቄ ነው:: ይህም እንደ ዐረፍተ ነገር ልተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “እኔ እግዚአብሔር አይደለሁም! ልጅ እንዳትወልጂ የሚከለክለው እኔ አይደለሁም” (ቅኔ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

Genesis 30:3

እርስዋም አለች

ራሔል አለች

እነሆ

“ተመልከት” ወይም “ስማ” ወይም “ሊናገር ስላለሁ ነገር ትኩረት ስጥ”

አገልጋዬ ባላ አለችልህ ……. ከእርስዋ ልጆች እንዳገኝ

በዚያን ጊዜ መካን ሴት በሕጋዊነት ልጅ የሚታገኝበት ተቀባይነት ያለው መንገድ ይህ ነው:: የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ባላ

የራሔል ሴት ባሪያ ስም ነው፡፡ በዘፍጥረት 29፡29 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

በጉልበቶቼ ወይም በጭኖቼ

ይህ ባላ የሚትወልደው ልጅ ለራሔል እንደሚሆን የሚገልጽ አባባል ነው:: አት: “ለእኔ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በእርሷ አማካኝነት ልጅ ይኖረኛል

በዚህ መንገድ ልጅ እንዲኖረኝ ታደርጋለች

Genesis 30:5

ባላ

የራሔል ሴት ባሪያ ስም ነው፡፡ በዘፍጥረት 29፡29 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ለያዕቆብ ወንድ ልጅ ወለደች

ለያዕቆብ ወንድ ልጅም ወለደችለት

ስሙንም አወጣችለት

ራሔል ስም አወጣችለት

ዳን ብላ ጠራችው

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ዳን የሚለው ስም ‘እርሱ ይፈርዳል’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 30:7

ባላ እንደገና ጸነሰች

ባላ እንደገና አረገዘች

ለያዕቆብ ሁለተኛ ወንድ ልጅ ወለደች

ለያዕቆብ ሁለተኛ ወንድ ልጅን ወለደችለት

ከእኀቴ ጋር ብርቱ ትግልን ታገልሁ

ትግልን ታገልሁ የሚለው ሀረግ አጽንዖትን የሚሰጥ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው ራሔል እንደ እኀትዋ አንድን ልጅ ለማግኘት ያደረገችው ከልያጋር አካላዊ ትግል እንዳደረገች የሚገልጽ ዘይቤያዊ አነጋገር ነው:: አት: “እንደ ታላቅ እኀቴ ልያ ልጅን ለማግኝት ትልቅ ተጋድሎ አድርጌያለሁ:: (ፈሊጣዊና ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ቻልኩኝ

አሸነፍሁ ወይም ተሳክቶልኛል

ስሙንም ንፍታለም ብላ አወጣችለት

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ንፍታለም የሚለው ስም ‘ትግሌ’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 30:9

ልያም ባየች ጊዜ

ልያም በተረዳች ጊዜ

አገልጋይዋን ዘለፋን ወሰደች ሚስት ትሆነውም ዘንድ ለያዕቆብ ሰጠችው

አገልጋይዋን ዘለፋን ሚስት እንዲትሆነው ለያዕቆብ ሰጠችው

ዘለፋ

የልያ ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29:24 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ለያዕቆብ ወንድ ልጅ ወለደች

ለያዕቆብ ወንድ ልጅን ወለደችለት

ምን ዓይነት መታደል ነው!

እንዴት ያለ መታደል ነው! ወይም ምን ዓይነት ዕድል ነው!

ስሙንም ጋድ ብላ አወጣችው

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ጋድ የሚለው ስም ‘እድለኛ’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 30:12

ዘለፋ

የልያ ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29:24 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ለያዕቆብ ሁለተኛ ወንድ ልጅ ወለደች

ለያዕቆብ ሁለተኛ ወንድ ልጅ ወለደችለት

ምነኛ ደስተኛ ሆንሁ!

እንዴት የተባረኩ ነኝ! ወይም እንዴት ደስተኛ ነኝ !

ሴቶች ልጆች

ሴቶች ወይም ልጃገረዶች/ወጣት ሴቶች

ስሙንም አሴር ብላ አወጣችለት

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “አሴር የሚለው ስም ‘ደስታ’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 30:14

ሮቤል ወደ ሜዳ ወጣ

ሮቤልም ወጣ

ስንዴ በሚታጨድበት ቀናት

ቀናት የሚለው አባባል በዓመት ውስጥ ያለ ወቅት ወይም ጊዜ የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው:: አት “በዓመት ስንዴ በሚታጨድበት ጊዜ” ወይም “ስንዴ በሚታጨድበት ወቅት” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እንኮይ

ከፍቅረኛ ጋር ለመተኛት ስሜት የሚያነሣሣና ፍሬን የሚጨምር የአትክልት ፍሬ ነው:: አት: “የፍቅር ፍሬ” (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ባሌን….ጥቂት ነገር ነውን?

ባሌን …. አይሰማሽምን? ይህ ራሔልን ለመቆጣት የተጠቀመችው ቅኔያዊ ጥያቄ ነው ይህ ጥያቄ በስድ ዐረፍት ነገር ሊገለጽ ይችላል:: ባሌን የማያስከፋ ነው:: (ቅኔ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ) …ደግሞ ሊትወስጂ አማረሽ? ይህንም ቅኔ አዘል ጥያቄ የተጠቀመችው ራሔልን ለመቆጣት ነው ይህ ጥያቄ በስድ ዐረፍት ነገር ሊገለጽ ይችላል:: አት: አሁን ደግሞ… አማረሽ! (ቅኔ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ከዚያም ይተኛ

“ከዚያም ያዕቆብ ይተኛ” ወይም “ያዕቆብ እንዲተኛ እፈቅዳለሁ”

Genesis 30:16

በልጄ እንኮይ

ለልጄ “እንኮይ” ዋጋ በዘፍጥረት 3ዐ;14 እንኮይ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ጸነሰች

አረገዘች

ለያዕቆብ አምስተኛ ወንድ ልጅ ወለደች

አምስተኛ ወንድ ልጅንም ለያዕቆብ ወለደች

እግዚአብሔር ዋጋዬን ከፈለልኝ

እግዚአብሔር ልያን መካሡ ለሚሠራው ሠራተኛ አንድ አለቃ ድርጐውን እንደሚከፍል እንደከፈለላት ተደርጐ ተገልጾአል “እግዚአብሔር የድርሻዬን ሰጠኝ” ወይም “እግዚአብሔር ካሠኝ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ስሙንም ይሳኮር ብላ አወጣችለት

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ይሳኮር የሚለው ስም ‘ካሣ አለ’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 30:19

ልያ አሁንም ደግሞ ጸነሰች

ልያ እንደገና አረገዘች

ለያዕቆብ ስድስተኛ ወንድ ልጅ ወለደች

ስድስተኛ ወንድ ልጅም ለያዕቆብ ወለደች

ስሙንም ዛብሎን አለችው

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ዛብሎን የሚለው ስም ‘ክብር’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ስምዋንም ዲና አለቻት

ይህ የልያ ሴት ልጅ ስምዋ ነው፡፡(ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 30:22

እግዚአብሔርም ራሔልን አሰባት ልመናዋንም ሰማ

አሰባት የሚለው አባባል አስተዋላት ማለት ነው:: ይህ እግዚአብሔር ራሔልን ረስቶአታል ማለት አይደለም:: ጥያቄዋን አሰበ ማለት ነው:: አት: “እግዚአብሔርም ራሔልን አሰበ የፈለገችውንም ሰጣት” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ኀፍረተን አስወገደልኝ

እግዚአብሔር ራሔል እንዳታፍር ያደረገው ሐፍረት አንድ ሰው ከአንድ ሰው ወስዶ እንደሚያስወግድ ዕቃ ተደርጐ ተነገሮአል:: ረቂቅ ስም ሐፍረት እንደ እፍረት ሊገለጽ ይችላል::

አት: እግዚአብሔር ከእንግዲህ ወዲህ እንዳላፍር አድርጐኛል፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር ወይም ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ) ስሙንም ዮሴፍ አለችው

ተረጓሚዎች የሚከተለውን አንደ ግርጌ ማስታወሻ ተጨማሪ አድርገው ሊያቀርቡ ይችላሉ:: “ዮሴፍ” የሚለው ስም ‘እርሱ ይጨምር’ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ሌላ ወንድ ልጅ ጨምሮ ይስጠኝ

የራሔል የመጀመሪያዎቹ ወንድ ልጆች ከሴት አገልጋይዋ ከባላ ነበር

Genesis 30:25

ራሔል ዮሴፍን ከወለደች በኋላ

ራሔልም ዮሴፍን ከወለደች በኋላ

እናም እመለስ ዘንድ

እንዲመለስ

እንዳገለገልሁህ ታውቃለህ

ያዕቆብ ላባንን የተስማሙበትን ኮንትራት ያስታውሳል (ዘፍጥረት 29 :27) ረቂቅ ስም “አገልግሎት” እንደ “አገለገለ” ሊገለጽ ይችላል:: አት: ለረጅም ጊዜያት እንዳገለገልሁህ ታውቃለህ:: (ረቂቅ ስሞች ይጠቀሙ)

Genesis 30:27

ላባንም እንዲህ አለው

ላባንም ያዕቆብን እንዲህ አለው

በአይንህ ፊት ሞገስን የማገኝ ቢሆን

አይኖች ማየትን ይወክላሉ እናም ማየት ሃሳብን ወይም ውሳኔን ይወክላል:: አት: “በአንተ ፊት ሞገስ ካገኘሁ” ወይም “በእኔ የተደሰትህ ከሆንህ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሞገስ ማግኘት

አንድ ሰው በሌላኛው ሰው ዘንድ ሞገስ ማግኘቱን የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው:: (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ቆይ ምክንያቱም

ተቀመጥ ምክንያቱም

በንግርት ተረድቸአለሁ

በመንፈሳዊና ማጅካዊ ልምምዶቼ ተረድቸአለሁና

በአንተ የተነሣ

በአንተ ምክንያት

ደመወዝህን ንገረኝ

ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት እዚሁ ላቆይህ ምን ያህል መክፈል እንዳለብኝ ንገረኝ፡፡ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 30:29

ያዕቆብም አለው

ያዕቆብ ላባንን አለው

ከብቶችህ በእኔ ጥበቃ ምን ያህል እንደተመቻቸው

ጥበቃ ከጀመርኩባቸው ጊዜ ከብቶች እንዴት እንደተመቻቸው

እኔ ከመምጣቴ በፊት ጥቂት ነበሩ

ለአንተ ሥራ ከመጀመረ በፊት መንጐችህ ጥቂት ነበሩ

እናም ይህ በመጨመር ተትረፍርፎአል

ነገር ግን አሁን ሀብትህ በጣም ጨምሮአል

አሁንም እኔ ደግሞ ለቤቴ የሚሆነውን የማቀርበው መቼ ነው?

አሁንም እኔ ደግም ለቤተሰቤ የምሠራው መቼ ነው? ያዕቆብ ለቤተሰቡ የሚሆነውን ማቅረብ እንዳለበት ለማጽናት ጥያቄ ይጠቀማል ይህም ጥያቄ በዐረፍተነገር መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “አሁን ለቤተሰበ የሚሆነውን ማሰብ አለብኝ” (ቅኔ አዘል ጥያቄችን ይመልከቱ)

Genesis 30:31

ታዲያ ምን ልስጥህ?

“ታዲያ ምን መክፈል እችላለሁ?” ወይም “ታዲያ ምን መስጠት እችላለሁ?” ይህ የበለጠውኑ ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት እንዲትቆይና እንዲትሠራልኝ ዘንድ ምን መክፈል እችላለሁ?(ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይጠቀሙ)

ይህንም ነገር ቢታደርግልኝ

ያዕቆብ ሊናገር ያለው እርሱ ከተናገረው ጋር እንደሚጻረር ለማሳየት አገናኝ ቃል “ነገር ግን” በመግቢያው ሊጠቀም ይቻላል:: አት: “ነገር ግን ይህንም ነገር ቢታደርግልኝ” (አገናኝ ቃላት ይመልከቱ)

ይህ ነገር

“ይህ ነገር” የሚለው ሀረግ ያዕቆብ በቁጥር 32 የሚያቀርበውን ያመለክታል::

መንጎችህን እመግባለሁ/አሠማራለሁ እጠብቃለሁ

መንጎችህን እመግባለሁ እጠብቃለሁ

ከበጐቹ መካከል ዝንጉርጉር የሆኑትን ነቁጣ ያለባቸውንና ጥቋቁሮቹን እንዲሁም ከፍዬሎች ነቁጣ ያለበቸውንና ዥንጉርጉሮቹን እለያለሁ

ማንኛውንም ዥንጉርጉርና ጥቁር የሆነውን በግና ዝንጉርጉር የሆነውን ፍዬል እለያለሁ

እነዚህ ደመወዜ ይሁኑ

እንዚህ እዚሁ ለሚቆየው ዋጋዬ ይሁኑ

Genesis 30:33

ታማኝነቴ ይታወቃል

ታማኝነት የሚለው ቃል አማንነት ማለት ነው ይህም ታማኝነት አንድ ሰው ሰለሌላኛው ሰው በመደገፍ ወይም በመቃወም የሚሰጠው ምሥክርነት እንደሆነ ይናገራል:: አት: “ለአንተ ታማኝ መሆነንና አለመሆነን በኋላ ታውቀዋለህ”:: (ሰውኛ አገላለጽ ይመልከቱ)

በመንጋቼ መካከል ዥንጉርጉር ወይም ነቁጣ የሌለበት ፍዬል ወይም ጥቁር ያልሆነ ቢገኝ ያ እንደተሰረቀ ይቆጠር

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ ገቢራዊ መንገድ ሊገለጽ ይችላል አት ማንኛውም ዥንጉርጉር ያለሆነ ፍዬልና ጥቁር ያልሆነ በግ ቢታገኘው እንደተሰረቀ መቁጠር ትችላለህ:: (ተሻጋሪና የማይሻገር ግሥ የያዙ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

እነሆ እንደቃልህ ይሁን

“እንደተናገርከው ይሁን” ወይም “አንተ እደተናገርከው እናደርጋለን”

Genesis 30:35

ሽመልመሌ የሆኑትን ወይም ነቁጣ ያለባቸውን

ሽመልመሌና ነቁጣ ያለባቸውን

ነቁጣ ያለባቸውንና ዥንጉርጉር የሆኑትን

ነቁጣ ያለባቸውን

ማንኛውንም ነጭ ያለበትን

ማንኛውም ነጭ ያለበት በግ

ከበጎች ሁሉ ጥቋቁር የሆኑትን

ጥቁር በጎችን ሁሉ

በእነርሱ እጅ ሰጣቸው

እዚህ “እጅ” “ቁጥጥር” ወይም “ጥበቃ” የሚተካ ነው:: አት: “ልጆቹ እንዲጠብቁ አደረጋቸው” (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 30:37

እርጥብ የልብን የለውዝንና የኤርሞን

እነዚህ ሁሉ ነጭ ዛፎች ናቸው:: (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቅርፊታቸውን ልጦ የበትሮቹ ውስጠኛው ነጩ አካል እንዲታይ አደረገ

የቅርፊታቸውን አንዳንድ ክፍሎችን በመላጥ የበትሮቹ ውስጠኛው ነጭ አካል እንዲታይ አደረገ

በማጠጫ ገንዳዎች

ከብቶችን ለማጠጣት ውሃን የሚይዙ ረጅምና ክፍት የሆኑ ገንዳዎች

Genesis 30:39

መንጋዎች ይሳረሩ ነበር

“የመንዎች እንስሳት ይጸልሱ ነበር” ወይም “ይጠቃቁ ነበር”

ሽመልመሌ ዝንጉርጉርና ነቁጣ የጣለባቸውን ግልገሎች ወለዱ

ዝንጉርጉርና ነቁጣ ያለባቸውን ግልገሎት ወለዱ

ያዕቆብም ለያቸው

ይህ ለብዙ ዓመታት እንደተረገ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ለሚቀጥሉት ብዙ ዓመታት ያዕቆብ ለያቸው” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ፊታቸውን መልሰው

ፊት ለፊት እያዩ

ከመንጋዎቹ ለራሰ ለያቸው

የራሱን መንጋ ለየ

Genesis 30:41

በመንጋዎች ዐይን ፊት

እዚህ የመንጋዎች ዐይን በጎችን ወይም መንጋዎችን የሚያመለክትና የሚያዩትን እንደሚያተኩር ነው:: አት: (መንጋው እንዲያየው ዘንድ (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉውን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በበትሮቹ መካከል

በበትሮቹ ፊትለፊት

በከሱ እንስሳት

በደካማዎች እንስሳት

ስለዚህ ደካማ ደካማዎቹ ለላባን ሲሆኑ ብርቱ ብርቱዎቹ ለያዕቆብ ሆኑ

ይህን ይበልጥኑ ግልጽ ማድረግ ይቻላል:: አት: “ደካማ ደካማዎቹ ዝንጉርጉርና ነቁጣ ስለሌላቸው ለላባን ሲሆኑ ብርቱ ብርቱዎች ዝንጉርጉርና ነቁጣ ስላላቸው ለያዕቆብ ሆኑ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 30:43

ይህ ሰው

ያዕቆብ

እጅግ ባለጠጋ ሆነ

“እጅግ በለጸገ” ወይም “ሀብታም ሆነ”


Chapter 31

1 የላባ ወንዶች ልጆች፣ “ያዕቆብ የአባታችንን ሀብት እንዳለ ወስዶታል፤ ይህ ሁሉ እርሱ ያከማቸውም ሀብት ከአባታችን የተገኘ ነው” እያሉ ሲያወሩ ያዕቆብ ሰማ። 2 በላባም ዘንድ እንደቀድሞ ተወዳጅ አለመሆኑን ተረዳ። 3 እግዚአብሔርም ያዕቆብን፣ “ወደ አባቶችህ ወደ ዘመዶችህ አገር ተመለስ፤ እኔም ከአንተ ጋር እሆናለሁ” አለው። 4 ስለዚህ ያዕቆብ መንጋዎቹ ወደ ተሰማሩበት መስክ እንዲመጡ ራሔልንና ልያን አስጠራቸው፤ 5 እንዲህም አላቸው፤ “አባታችሁ ስለ እኔ ያለው አመለካከት እንደ ቀድሞ አለመሆኑን ተረድቻለሁ፤ ቢሆንም የአባቴ አምላክ አልተለየኝም፤ 6 መቼም ባለኝ አቅም አባታችሁን ማገልገሌን እናንተ ታውቃላችሁ። 7 አባታችሁ ደመወዜን ዐሥር ጊዜ እየለዋወጠ አታልሎኛል፣ ሆኖም እንዲጎዳኝ እግዚአብሔር አልፈቀደለትም። 8 እርሱ፣ ‘ደመወዝህ ዝንጉርጉሮቹ ይሆናሉ ሲለኝ፣ መንጎቹ ሁሉ ዝንጉርጉር ወለዱ’፤ ደግሞም፣ ‘ደመወዝህ ሽመልመሌዎቹ ይሆናሉ ሲለኝ፣ መንጎቹ ሁሉ ሽመልመሌ መልክ ያላቸውን ወለዱ፤ 9 ስለዚህ እግዚአብሔር የአባታችሁን ከብቶች ወስዶ ለእኔ ሰጠኝ። 10 እንስሳቱ በሚጠቁበት ወራት የሚያጠቋቸው አውራ ፍየሎች ሽመልመሌ፣ ዝንጉርጉርና ነቁጣ መሆናቸውን በሕልም አየሁ። 11 በዚያው ሕልም የእግዚአብሔር መልአክ፦ ‘ያዕቆብ’ ብሎ ጠራኝ፣ እኔም ‘እነሆ አለሁ’ አልሁ። 12 እርሱም እንዲህ አለኝ፦ ‘መንጋዎቹን የሚያጠቋቸው አውራ ፍየሎች ሽመልመሌ፣ ዝንጉርጉርና ነቁጣ ያለባቸው መሆናቸውን ተመልከት፣ ላባ የፈጸመብህን በደል አይቻለሁ። 13 የድንጋይ ሐውልት በማቆም ዘይት ቀብተህ የተሳልህባት የቤቴል አምላክ እኔ ነኝ፤ አሁንም ይህን አገር ፈጥነህ ልቀቅ ወደ ተወለድህበትም ምድር ተመልሰህ ሂድ’ አለኝ።” 14 ራሔልና ልያም እንዲህ ብለው መለሱለት፦ “ከአባታችን የምንወርሰው ድርሻ አለን? 15 እርሱ እኛን የሚያየን እንደ ባዕዳን አይደለምን? ደግሞም እኮ እኛን ሽጦናል፣ የተሸጥንበትንም ዋጋ ራሱ በልቶታል። 16 እግዚአብሔር ከአባታችን ወስዶ ለአንተ የሰጠው ሀብት ሁሉ የእኛና የልጆቻችን ነው፤ ስለዚህ እግዚአብሔር የነገረህን ሁሉ አድርግ።” 17 ከዚያም ያዕቆብ ተነሥቶ ልጆቹንና ሚስቶቹን በግመሎች ላይ አስቀመጠ፤ 18 በመስጴጦምያ ካፈራው ሀብት ሁሉ ጋር ከብቶቹን በሙሉ ወደፊት አስቀደመ፣ ወደ አባቱም ወደ ይስሐቅ አገር፣ ወደ ከነዓን ምድር ጉዞውን ቀጠለ። 19 ላባ በጎቹን ሊሸልት ሄዶ ስለነበር፣ እርሱ በሌለበት ራሔል ከቤት የነበሩትን የአባቷን ጣዖቶች ሰርቃ ሄደች። 20 ያዕቆብ መሄዱን ለላባ ሳይገልጥለት አታሎት ሄደ፣ 21 የራሱ የሆነውን ሀብት ይዞ በፍጥነት ታጓዘ፤ የኤፍራጥስንም ወንዝ ተሻግሮ ወደ ኮረብታማው አገር ወደ ገለዓድ ሄደ። 22 ያዕቆብ መኮብለሉን ለላባ በሦስተኛው ቀን ተነገረው። 23 ከዘመዶቹ ጋር ሆኖ ያዕቆብን ተከታተለው፤ ሰባት ቀን ከተጓዙ በኋላ ገለዓድ በተባለው ተራራማ አገር ላይ ሊደርስበት ተቃረበ። 24 በዚያን ሌሊት እግዚአብሔር ለላባ በሕልም ተገለጠለትና “ያዕቆብን ክፉም ሆን ደግ እንዳትናገረው ተጠንቀቅ” አለው። 25 ያዕቆብ ገለዓድ በተባለው ኮረብታማ ስፍራ ድንኳኑን በመትከትል ሰፍሮ ሳለ ላባ ደረሰበት፤ ላባና ዘመዶቹም እዚያው ድንኳናቸውን ተክለው ሰፈሩ። 26 ከዚህ በኋላ ላባ ያዕቆብን እንዲህ አለው፦ “ስለምን እንዲህ አድርገህ አታለልኸኝ፤ ሴቶች ልጆቼንስ በጦርነት እንደተማረኩ ያህል ይዘሃቸው ለምን ሄድህ? 27 ሳትነግረኝ ተሰውረህ በመሄድ ለምን አታለልኽኝ? ነግረኸኝ ቢሆን በከበሮና በመስንቆ እየተዘፈነ በደስታ በሸኘሁህ ነበር። 28 ልጆቼንና የልጅ ልጆቼን በመሳም እንድሰናበታቸው ባለማድረግህ የሞኝነት ተግባር ፈጽመሃል። 29 ጉዳት ሳደርስብህ እችል ነበር፣ ነገር ግን ባለፈው ሌሊት የአባትህ አምላክ፣ ‘ያዕቆብን ክፉም ሆነ ደግ አንድ ቃል እንዳትናገረው’ ብሎ አስጠነቀቀኝ፣ 30 ወደ ትውልድ አገርህ ለመመለስ ባለህ ብርቱ ፍላጎት እንደተለየኸኝ አውቃለሁ፣ ታዲያ የቤቴን ጣዖቶች የሰረቅኽብኝ ለምንድነው?” 31 ለላባ እንዲህ ሲል መለሰለት፦ “ሴቶች ልጆችህን በኃይል ነጥቀህ ታስቀርብኛለህ ብዬ ስለ ፈራሁ ነው በድብቅ የሄድኩት። 32 ነገር ግን ከእኛ መካከል የአንተን የጣዖት ምስል የሰረቀ ሰው ካለ ይሙት። የአንተ የሆነ አንዳች ነገር ከኔ ዘንድ ቢገኝ፣ አንተው ራስህ ዘመዶቻችን ባሉበት ፈልግና ውሰድ።” እንደዚህ ሲል ራሔል የጣዖታቱን ምስል መስረቋን ያዕቆብ አያውቅም ነበር። 33 ላባም ወደ ያዕቆብ ድንኳንና ወደ ልያ ድንኳን እንዲሁም ወደ ሁለቱ ደንገጡሮቹ ድንኳን ገባ፤ ነገር ግን ምንም አላገኘም። ከልያ ድንኳን ከወጣ በኋላ ወደ ራሔል ድንኳን ገባ። 34 ራሔል ግን ጣዖቱቹን ወስዳ በግመሉ ኮርቻ ሥር በመሰወር በላያቸው ተቀምጣባቸው ነበር። ላባ በድንኳኑ ውስጥ ያለውን ጓዝ ሁሉ በርብሮ ምንም ነገር አላገኘም። 35 ራሔልም አባቷን፦ “በፊትህ ተነሥቼ መቆም ስላልቻልሁ፣ ጌታዬ አትቆጣ የወር አበባዬ መጥቶ ነው” አለችው፤ ስለዚህ በረበረ፤ የጣዖቱን ምስል ግን ማግኘት አልቻለም። 36 በዚህ ጊዜ ያዕቆብ ተቆጣ፤ ላባንም እንዲህ ሲል ወቀሰው፦ “እስቲ ወንጀሌ ምንድን ነው? ይህን ያህል የምታሳድደኝ ኃጢአቴ ምን ቢሆን ነው? 37 ዕቃዬን አንድ በአንድ በርብረሃል፤ ታዲያ የአንተ ሆኖ ያገኘኸው ዕቃ የትኛው ነው? ካለ፣ እስቲ በአንተም በእኔም ዘመዶች ፊት አቅርብና እነርሱ ያፋርዱን። 38 ሃያ ዓመት አብሬህ ኖሬአለሁ፤ በጎችህና ፍየሎችህ አልጨነገፉም፤ ከመንጋህም አንድ ጠቦት እንኳ አልበላሁም። 39 አውሬ የሰበረውንም ቢሆን እተካ ነበር፣ በቀንም ሆነ በሌሊት የተሰረቁትን ሁሉ ስታስከፍለኝ ኖረሃል። 40 ብዙ ጊዜ በቀን ሐሩርና በሌሊት ቁር እሠቃይ ነበር፤ በቂ እንቅልፍ ያገኘሁበት ጊዜ አልነበረም። 41 ሃያ ዓመት በቤትህ የኖርሁት በዚህ ሁኔታ ነበር፤ ዐሥራ አራት ዓመት ለሁለቱ ልጆችህ ብዬ አገለገልሁ፤ ስድስት ዓመት ስለመንጋዎችህ ስል አገለገልሁ፤ ይህም ሆኖ ደመወዜን ዐሥር ጊዜ ለዋውጠኽብኛል። 42 የአባቴ አምላክና እርሱም የሚፈራው የአብርሃም አምላክ ከእኔ ጋር ባይሆን ኖሮ ባዶ እጄን ሰድደኸኝ ነበር፤ እግዚአብሔር ግን መከራዬን ዐይቶ፣ ልፋቴን ትመልክቶ ትናንት ሌሊት ገሠጸህ።” 43 ላባም ለያዕቆብ እንዲህ ሲል መለሰ፤ “እነዚህ ሴቶች የእኔው ልጆች ናቸው፤ ልጆቻቸውም የእኔ ናቸው፤ እነዚህም መንጋዎች የእኔ ናቸው፤ ይህ የምታየው ሁሉ የራሴ ነው፤ ታዲያ በእነዚህ ሴቶች ልጆቼና በወለዷቸው ልጆቻቸው ላይ ዛሬ ምን ማድረግ እችላለሁ? 44 በል አሁን ቃል ኪዳን እንጋባ፤ ኪዳኑም በአንተና በእኔ መካከል ምስክር ይሁን።” 45 ያዕቆብም ድንጋይ ውስዶ ሐውልት አድርጎ አቆመው፤ 46 ከዚያም ዘመዶቹን “ድንጋይ ሰብስቡ” አላቸው። እነርሱም ድንጋይ እያመጡ ከመሩ፤ በክምሩም አጠገብ ምግብ በሉ። 47 ላባም ክምር ድንጋዩን ይጋርሠሀዱታ ብሎ ጠራው፤ ያዕቆብ ደግሞ ገለዓድ አለው። 48 ላባም “ይህ ክምር ድንጋይ በእኔና በአንተ መካከል ዛሬ ምስክር ነው” አለው። ገለዓድ ተብሎ የተጠራውም በዚሁ ምክንያት ነው፤ 49 ደግሞም ምጽጳ ተባለ ምክንያቱም ላባ እንዲህ ብሎአልና፤ “እንግዲህ ከዚህ በምንለያይበት ጊዜ እግዚአብሔር እኔንና አንተን ይጠብቀን፤ 50 ልጆቼን ብትበድላቸው ወይም ሌሎችን በላያቸው ብታገባ፣ ማንም ከእኛ ጋር ባይኖርም እንኳ እግዚአብሔር በአንተና በእኔ መካከል ምስክር መሆኑን አትርሳ።” 51 ላባም ያዕቆብን እንዲህ አለው፦ “ክምር ድንጋዩ እነሆ፤ በአንተና በእኔ መካካል ያቆምሁትም ሐውልት እነሆ፤ 52 ይህን ክምር ድንጋይ አልፌ አንተን ለማጥቃት ላልመጣ፣ አንተም ይህን ክምር ድንጋይና ይህን ሐውልት አልፈህ እኔን ለማጥቃት ላትመጣ፤ ይህ ክምር ድንጋይ ምስክር ነው፤ ይህም ሐውልት ምስክር ነው። 53 የአብርሃም አምላክ፣ የናኮር አምላክ፣ የአባታቸውም አምላክ በመካከላችን ይፍረድ።” ስለዚህ ያዕቆብ አባቱ ይስሐቅ በሚፈራው በእግዚአብሔር ማለ። 54 ያዕቆብ በኮረብታማው አገር ላይ መሥዋዕት አቀረበ፤ ዘመዶቹንም ምግብ እንዲበሉ ጋበዛቸው፤ እነርሱም ከበሉ በኋላ እዚያው አደሩ። 55 በማግስቱም ማለዳ ላባ የልጅ ልጆቹን እንዲሁም ሴቶች ልጆችን ስሞ መረቃቸው፤ ከዚያም ወደ አገሩ ተመለሰ።



Genesis 31:1

ይህን

ይህ ቃል የታሪኩን ትረካ መሥመር ለማቋረጥ ተጠቅሞአል በዚህ ጸሐፊው አዲስ ታሪክ ይጀምራል

ያዕቆብ የላባን ወንዶች ልጆች ያሉትን ነገር ሰማ

ያዕቆብ የላባን ወንዳች ልጆች የሚሉትነ ሰማ

ያዕቆብ የአባታችን የሆነውን ሁሉ ወስዶታል

የላባን ወንዶች ልጆች ከመቆጣታቸው የተነሣ አጋንነው ይናገራሉ አት ያዕቆብ የወሰደው ነገር ሁሉ የአባታችን ነበር:: (ማጋነንና ገሃዳዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ያዕቆብም የላባን ፊት አየ አመለካከቱም እንደተለወጠበት ተገናዘበ

አነዚህ ሁለት ዐረፍተ ነገሮች በመሠረት አንድ ናቸው:: ሁለተኛው ያዕቆብ በላባን ፊት ያየውን ይገልጻል:: አት: “ያዕቆብም ላባን እንዳለተደሰተበት ተረዳ” (ተጓዳኝ ንጽጽር ይመልከቱ)

አባቶችህ

አባትህ ይስሐቅና አያትህ አብርሃም

Genesis 31:4

ያዕቆብም ልኮ ራሔልንና ልያን ወደ በጎቹ ሥፍራ ወደ ሜዳ ጠራቸው

ያዕቆብ መንጎቹ ወደተሠማሩበት መስክ እንዲመጡ ራሔልንና ልያን አስጠራቸው

ለመንጋው እናም እንዲህ አላቸው

እነዚህ ሁለት አጫጭር ዐረፍተ ነገሮች ናቸው:: አት “ለመንጋው:: እንዲህም አላቸው” (የዐረፍተ ነገር ውቅር ይመልከቱ)

አባታችሁ ስለእኔ ያለው አመለካከት እንደቀድሞው አለመሆኑን ተረድቻለሁ

አባታችሁ በእኔ ደስተኛ እንዳልሆነ ተረድቻለሁ

ባለኝ ጉልቤቴ ሁሉ አባታችሁን እንዳገለገልሁ እናንተ ታውቃላችሁ

እናንተ የሚለው ቃል ራሔልንና ልያን ያመለክታል እንዲሁም ደግሞ ትኩረትን ይጨምራል፡፡ አት፡ “አባታችሁን ባለኝ ጉልበት ሁሉ እንዳገለገልሁ እናንተው ራሳችሁ ታውቃላችሁ” (ሁለተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 31:7

አታልሎኛል

ዋሽቶኛል ወይም በፍትሃዊነት አላስተናገደኝም

ደመወዜ

ሊከፍለኝ የተናገረውን

ሊጐዳኝ

ተገቢ ትርጉሞች 1 አካላዊ ጥቃት በማንኛውም መንገድ ለያዕቆብ መከራ መንስሄ በመሆን

ነቁጣ እንስሳት

ነጭ ምልክት ያላቸው እንስሳት

መንጎቹ ወለዱ

በጎቹ ወለዱ

ዝንጉርጉር

ዝንጉርጉር ቀለም ያላቸው እንስሳት

በዚህ መንገድ እግዚአብሔር የአባታችሁን ከብቶች ወስዶ ለእኔ ሰጠኝ

ይህም እንዴት እግዚአብሔር የአባታችሁን እንስሳት ለእኔ እንደሰጠኝ ነው

Genesis 31:10

አጠቃላይ መረጃ

ያዕቆብ ታሪኩን ለሚስቶቹ ለልያና ለራሔል መናገሩን ይቀጥላል

የሚጠቁበት ወራት በሚሆንበት ጊዜ

በሚጠቁበት ወራት

መንጋው በሚጠቃበት

እዚህ “መንጋው” ሴት ፍዬሎችን ያመለክታል:: አት: “ሴት ፍዬሎች በሚጠቁበት” (ክፍልን ለሙሉና ሙሉውን ለክፍል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ሽመልመሌ ዝንጉርጉርና ነቁጣ

ዝንጉርጉር ትንሽ ነቁጣና ትልቅነቁጣ ያላቸው

የእግዚአብሔር መልአክ

ተገቢ ትርጉሞች 1) እግዚአብሔር በሰው መልክ ሲገለጥ 2) ከእግዚአብሔር መልእክተኞች አንዱሲገለጥ ሀረጉ በተክክል እስካልተገለጸ ለ”መልአክ” የሚንጠቀመውን መደበኛ ቃል በመጠቀም በቀላሉ እንደ “እግዚአብሔር መልእክተኛ” መተረጐም ተገቢ ነው::

እኔም አልሁ

እኔም መለስሁ

እነሆኝ

አዎን እየሰማሁ ነኝ ወይም አዎን ምንድነው? በዘፍጥረት 22: 1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

Genesis 31:12

አጠቃላይ መረጃ

የእግዚአብሔርም መልአክ ያዕቆብን መናገር ቀጠለ:: (ዘፍጥረት 31:1ዐ ይመልከቱ)

ዐይኖችህን ቀና አድርግ

ይህ ቀና ብለህ ተመልከት ማለት ነው (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

መንጎቹን የሚያጠቋቸውን

እዚህ “መንጋ” እንስት ፍዬሎች ብቻ ያመለክታል:: አት “የመንጋው እንስት ፍዬሎችን የሚያጠቋቸውን” (ክፍል ለሁሉና ሁሉን ለክፍል የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ሽመልመሌ ዝንጉርጉርና ነቁጣ

ዝንጉርጉርና ነቁጣ ያለባቸው

ዘይት የቀባሄው ሐውልት

ያዕቆብም ሐውልቱን ዘይፍ በመቀባት ለእግዚአብሔር የቀደሰው (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

የትውልድህ ምድር

የተወለድህበት ምድር

Genesis 31:14

ራሔልና ልያም እንዲህ ብለው መለሱ

ይህ በተመሣሣይ ጊዜ ተናግረዋል ማለት አይደለም እንተስማሙ ያጸናል

ከአባታችን ሀብት የሚናገኘው ምን ድርሻ ወይም ውርስ አለን?

ራሔልና ልያ በጥያቄ መልክ አባታቸው ሊሰጣቸው ምንም እንዳልቀረ አጥብቀው ይናገራሉ፡፡ አት፡ “ከአባታችን ልንወርሰው በፍጹም የቀረ ምንም ነገር የለም!” (ቅኔ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

እኛን የሚያየን እንደባዕድ አይደለምን?

አባታቸው እንዴት እንደሚያዩአቸው ያላቸውን ቁጣ በጥያቄ ይገልጸሉ:: አት: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ገቢራዊ ዓረፍተ ነገር ሊገለጽ ይችላል አት አባታችን እንደ ሴት ልጆቹ ሳይሆን እንደባዕድ ሴቶች ያየናል:: (ቅኔ አዘል ጥያቄዎችና ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮች ይመልከቱ)

ሽጦናል

ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: ለራሱ ጥቅም ሽጦናል:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ደግሞም ዋጋችንን በፍጹም በልቶታልና

ላባን ለሴት ልጆቹ መስጠት የነበረበትን ገንዘብ በፍጹም ለራሱ መጠቀሙ የዱር አራዊት እንደ ምግብ ገንዘቡን እንደበሉት ተደርጐ ተነግሮአል:: አት: “በፍጹም ገንዘባችንን ተጠቅሞአል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይጠቀሙ)

ሁሉ የእኛና የልጆቻችን ነው

ለእኛና ለልጆቻችን ይገባል

አሁንም

እዚህ አሁን የአሁን ጊዜ አይደለም ነገር ግን ለሚከተለውን አስፈላጊ ነጥብ ትኩረት ለመስጠት ነው፡፡

እግዚአብሔር ያለህን ሁሉ አድርግ

እግዚአብሔር የነገረህን ሁሉ አድርግ

Genesis 31:17

ወንዶች ልጆቹ

ያዕቆብ ልጆቹን ሁሉ ወሰደ:: ወራሾች ስለሆኑ ወንዶች ልጆቹን ብቻ የጠቀሳል:: አት: “ልጆቹን” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ከብቶቹን ሁሉ ነዳ

ሁሉን ከብቶች ነዳ:: እዚህ “ከብቶች” ሁሉን የቤት እንስሳትን ይወክላል፡፡

በጳዳን አራም ካፈራው ሀብት ሁሉ ጋር

በጳዳን አራም እያለ ያፈራቸውን ሌሎች ከብቶችንም

ከዚያም ወደ አባቱም አገር ወደ ይስሐቅ ወደ ከነዓን ጉዞውን ቀጠለ

አባቱ ይስሐቅ ወደሚኖርበት አገር ወደ ከነዓን ሄዴ

Genesis 31:19

ላባን በጐቹን ሊሸልት ሄዶ ሳለ

ላባን የበጐቹን ጸጉር ሊያስቆርጥ በሄደበት ጊዜ

ወንዙን

የኤፍራጥሰ ወንዝ ያመለክታል

አመራ

ተጓዘ

ወደ ኮረብታማው አገር ወደ ገለአድ

ወደ ገለአድ ተራራዎች ወይም ወደ ገለአድ ተራራ

Genesis 31:22

በሶስተኛው ቀን

የወጡበትን ቀን እንደ አንድ ቀን መቁጠር የአይሁድ ለማድ ነው:: አት: “ከወጡበት ሁለት ቀናት በኋላ”

ለላባን ተነገረው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት አንድ ሰው ለላባን ነገረው ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮች ይመልከቱ

ያዕቆብም ኮበለለ

የቤተሰቡ መሪ ስለሆነ ያዕቆብ ብቻ ተጠቅሶአል ቤተሰቡ ከእርሱ ጋር እንደተጓዙ ግልጽ ማድረግ ይቻላል:: አት: “ያዕቆብ ከሚስቶቹና የልጆቹ ጋር ኮበለለ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ይዞ ተነሣ

ላባን ይዞ ተነሣ

ተከታተለው

አሳደደው

ለሰባት ቀናት ጉዞ

ያዕቆብን ደርሶ ለመያዝ ላባን ሰባት ቀናት ተጓዘ

ደረሰበት

ያዘው

Genesis 31:24

ከዚያም እግዚአብሔር ለሶሪያዊው ለላባን በሕልም ተገልጦ

“ከዚያም” የሚለው ቃል የተጠቀመው ታሪኩን ወደ ላባን የሕይወት ዳራ መረጃ ለመቀየር ነው አት: “በዚያ ሌሊት እግዚአብሔር ለላባን ተገልጦ” (የዳራ መረጃዎች ይመልከቱ)

ያዕቆብን ክፉም ሆነ ደግ እንዳትናገረው ተጠንቀቅ አለው

“ክፉ ሆነ ደግ” የሚለው ሀረግ የተጠቀመው “ምንም” ለማለት ነው፡፡ አት፡ ያዕቆብን ከመሄድ ለማቋረጥ ለመሞከር ምንም ነገር እንዳትናገር (See: Merism)

ከዚያም ያዕቆብ ገለዓድ በተባለው ኰረብታማ አገር ድንኳን ተክሎ ሳለ ላባ ደረሰበት ላባና ዘመዶቹ በዚያው ሠፈሩ::

“ከዚያም” የሚለው ቃል የተጠቀመው ታሪኩን ወደ ያዕቆብናላባን የሕይወት ዳራ መረጃ ለመቀየር ነው:: አት: “ላባን ያዕቆብን በደረሰበት ጊዜ ያዕቆብ በኰረብታማው አገር ድንኳን ተክሎ ነበር: ከዚያም ላባንና ዘመዶቹ ደግሞ በኰረብታማው ገለዓድ አገር ድንኳን ተከሉ” (የዳራ መረጃዎች ይመልከቱ)

Genesis 31:26

ልጆቼን የጦር ምርኮኛ ይመስል አካልበህ ወሰድናቸው

ያዕቆብ ቤተሰቡን ከራሱ ጋር ወደ ከነዓን ምድር መውሰዱ ልክ ያዕቆብ እንደ የጦር ምርኮኞችን እናም አሰገድዶአቸው እየወሰደ እንዳለ ላባን ይናገራል ላባን ስለተቆጣና ያዕቆብ ስላደረገው ነገር ጸጸት እንዲሰማው አግንኖ ይናገራል:: (ተመሣሣይ ንጽጽር የማጋነንና ገሃዳዊ አገላለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ተደብቀህ ሄድህ

በድብቅ ሸሸህ

ፍስሐ በማድረግ

በደስታ

በከበሮ/ ታምቡርና በበገና

እነዚህ መሣሪያዎች ሙዝቃን የሚገልጹ ናቸው፡፡ አት፡ “እናም በሙዝቃ” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ታምቡር

የከበሮ ዓይነት ለምት የሚሆን አናት ያለው ዙሪያሙ ከብረት የተሠራና መሣሪያው በሚመታበት ጊዜ የሚርገበገብ የሙዝቃ መሣሪያ ነው ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ

ወንዶች የልጅ ልጆቼን እንዲስማቸው

እዚህ ወንዶች የልጅ ልጆች ወንድ ሆነ ሴት ሁሉን የልጅ ልጆችን ይወክላሉ:: አት: “የልጅ ልጆቼን እንዲስማቸው” (በወንዴ ጾታ የተጠቀሱ ሴት ጾታንም የመግለጽ አባባል ይመልከቱ)

አሁን የሠራሄው የጅል ሥራ ነው

በጅልነት አድርገሄዋል

አሁንም

ይህ የዚያን ጊዜ ማለተ አይደለም ነገር ግን ለሚከተለውን ጠቃሚ ነገር ትኩረት እንደሰጥበት ነው

Genesis 31:29

እናንተን ልጐዳችሁ ነበር

እዚህ “እናንተ” ብዙና ከያዕቆብ ጋር ያሉትን ሁሉ ያመለክታል:: አት: “ሊጐዳችሁ የሚያስችለኝ ከእኔ ጋር ብዙ ሰዎች ነበሩ” (የሁለተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ያዕቆብን ክፉም ሆነ ደግ እንዳትናገረው ተጠንቀቅ አለኝ

“ክፉ ሆነ ደግ” የሚለው ሀረግ የተጠቀመው “ምንም” ለማለት ነው፡፡ በዘፍጥረት 31:24 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት፡ “ያዕቆብን ከመሄድ ለማቋረጥ ለመሞከር ምንም ነገር እንዳትናገር” (See: Merism)

አንተም ሄደሃል

አንተ የሚለው ነጠላና ያዕቆብን ያመለክታል:: (የሁለተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ወደ አባትህም ቤት

እዚህ ቤት ቤተሰብን ይወክላል:: አት: “ወደ አባትህና ሌሎች ቤተሰብህ ቤት ለመመለስ” (ክፍልን ሙሉና ሙሉውን ክፍል አድርጐ የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

አምላኮቼን

ጣዖቶቼን

Genesis 31:31

ልጆችህን ከእኔ የምትቀማ ስለመሰለኝና ስለፈራሁ በድብቅ ወጣሁ፡፡

በድብቅ የወጣሁት ልጆችህን ከእኔ ነጥቀህ ታስቀርብኛለህ ብዬ ስለፈራሁ ነው፡፡

ከእኛ መካከል የአንተን የጣዖታት ምስል ደብቆ የተገኘ ሰው ካለ ይሙት

ይህ በአዎንታዊ መንገድ መገለጽ ይችላል አት ጣዖቶችህን የሰረቀ ማንም ቢገኝ እንገድላለን (ምጸት ይመልከቱ)

ዘመዶቻችን/የእኛ ዘመዶች ባሉበት

የእኛ የሚለው ቃል የያዕቆብ ዘመዶችንና የላባን ዘመዶች ያመለክታል:: ሁሉም ዘመዶች ፍትሃዊና ግልጽ መሆኑን ለማረጋገጥ ያዩታል (ሁሉ አቀፍ አንደኛ ወገን አገላለጽ ይመልከቱ)

ያንተ የሆነ አንዳች ነገር ከኔ ዘንድ ቢገኝ ውሰድ

በእኛ ዘንድ ካለው ያንተ የሆነውን ፈልግና ውሰድ

ያዕቆብ ራሔል እነዚያን/ጣዖታቱን መስረቋን አያውቅም ነበር

ይህም ታሪኩን ወደ ያዕቆብ ሕይወት ዳራ መረጃ ይቀይራል (የዳራ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 31:33

ሁለቱ ደንገጡሮቿ

ዘለፋንና ባላን ያመለክታል

አላገኛቸውም

ጣዖታቱን አላገኘም

Genesis 31:34

ከዚያም ራሔል በላያቸው ተቀምጣ ነበር

ከዚያም የሚለው ቃል ታሪኩን ወደ ራሔል ሕይወት ዳራ መረጃ የቀይራል (የዳራ መረጃ ይመልከቱ)

ኮርቻ

ሰው እንዲቀመጥበት በጋማ እንስሳት ጀርባ የሚደረግ መቀመጫ ነው

ጌታዬ

አንድን ሰው “ጌታዬ” ብሎ መጥራት የማክበር መንገድ ነው

በፊትህ ተነስቼ መቆም ስላልቻልሁ

ይህ ከማሕጸንዋ ወራዊ ደም የሚፈስበት ጊዜ ውስጥ እንዳለች ያለመክታል:: (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ መንገድ በተዘዋዋሪ አንድን ነገር ስለመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 31:36

እርሱም እንዲህ አለው

ያዕቆብ ላባንን እንዲህ አለ

ወንጄሌ ምንድነው? ይህን ያህል የምታሳድደኝ ኃጢአቴ ምን ቢሆን ነው?

ወንጄሌ ምንድነው እና ኃጢአቴ ምን ሆን የሚሉ ሀረጐች በመሠረቱ ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው ያዕቆብ ላባንን ምን ስህተት እንደሠራ ይጠይቀዋል አት ይህን ያህል በጽኑ የምታሳድደኝ ምን ስህተት ቢፈጽም ነው? (ተጓዳኝ ተነጻጻሪ አባባል ይመልከቱ)

በጽኑ

እዚህ “ጽኑ” የሚለው ቃል ላባን በማጣደፍ ያዕቆብን ለመያዝ ባለው ተነሣሽነት እንዳሳደደው ይገልጻል (ፈሊጣዊ አባባል ይመልከቱ)

ከቤትህስ ዕቃ ሁሉ ምን አገኘህ?

ያንተ ሆኖ ያገኘሄው ዕቃ የትኛው ነው?

በእኛ ዘመዶች ፊት አቅርብ

እዚህ እኛ የሚለውቃል የያዕቆብ ዘመዶችና የላባንን ዘመዶች ያመለክታል:: አት: ያገኘሄውን ማንኛውንም ነገር በዘመዶቻችን ፊተ አቅርብ (አካታች አንደኛ ወገን አገላለጽ ይመልከቱ)

እነርሱ ሁለታችንን ይፍረዱ ወይም እነርሱ ይፍረዱን

እዚህ “ሁለታችን” ያዕቆብንና ላባን ያመለክታል:: “ይፍረዱን” የሚለው አባባል ከክርክሩ የትኛው ትክክል እንደሆነ ይወስኑ ማለት ነው፡፡

Genesis 31:38

አጠቃላይ መረጃ

ያዕቆብ ለላባን መናገሩን ቀጠለ

ሃያ ዓመታት

2ዐ ዓመታት (ቁጥሮች ይመልከቱ)

ሴት በግ

እንስት የበግ ጠቦት

አልጨነገፉም

በእርግዝና ወቅት የተቀጨ ወይም ሞቶ የተወለደ ጠቦት አልነበረም ማለት ነው

በአውሬ የተሰበረውን አምጥቼ አላውቅም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊገለጽ ይችላል አት አውሬ ከእንሰሳትህ አንዱን በገደለ ጊዜ በድኑን ለአንተ አምጥቼ አላውቅም (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ያጣሄውን እተካ ነበር

ያዕቆብ ከመንጋው የላባንን ሙት እንስሳት ምትክ መቁጠር በጫንቃው እንደተሸከመው ሽክም እንደነበር ተደርጐ ተገልጾአል:: አት: “ከመንጋህ እንደጠፋ ከመቁጠር ከመንጋዬ እንደጠፋ ቆጥረዋለሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በቀን በሐሩር ሌሊት በቁር ይበላኝ ነበር

በሞቃትና ቀዝቃዛ የአየር ሁኔታ መሠቃየት የአየር ሁኔታዎች ያዕቆብ እንደ አውሬዎች እንደበሉ ተደርጐ ተገልጾአል:: አት በቀን ሐሩርና በሌሊት ቁር ከመንጋዎችህ ጋር ነበርሁ (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 31:41

አጠቃላይ መረጃ

ያዕቆብ ለላባን መናገሩን ቀጠለ

እነዚህ ሃያ ዓመታት

እነዚህ 2ዐ ዓመታት (ቁጥሮች ይመልከቱ)

አሥራ አራት ዓመታት

14 ዓመታት (ቁጥሮች ይመልከቱ)

ደመወዘን አሥር ጊዜ ለዋውጠህብኛል

መክፈል ያለበትን አሥር ጊዜ ለዋውጦብኛል:: በዘፍጥረት 31:7 ደመወዜን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

የአባቴ አምላክ የአብርሃም አምላክ የይስሐቅም ፍርሃት ከእኔ ጋር ባይሆን ኖሮ

የአብርሃምና የአባቴ የይስሐቅ አምላክ ከእኔ ጋር ባይሆን ኖሮ

የአባቴ አምላክ

እዚህ “አባቴ” የሚለው ቃል አባቱን ይሰሐቅን ያመለክታል::

ይስሐቅ የሚፈራው

እዚህ “ፍርሃት” ለእግዚአብሔር ያለውን ፍርሃት ያመለክታል፡፡

ባዶ እጄን

ይህ ምንም አለመኖር ማለት ነው:: አት: “ፍጹም ባዶ” (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

እግዚአብሔር መከራዬን አይቶ ልፋቴን ተመልክቶ

መከራ የሚለው ረቂቅ ስም መከራ አየ በሚቶል ሊገለጽ ይችላል:: አት: “እግዚአብሔር ልፋቴን አይቶ እንዴት መከራ እንዳሳየሄኝ ተመልክቶ” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

Genesis 31:43

ነገር ግን በእነዚህ ሴቶች ልጆቼና በወለዷቸው ልጆቻቸው ላይ ዛሬ ምን ማድረግ እችላለሁ?

ላባን ምንም ማድረግ እንደማይችል አግንኖ ለመቅለጽ ጥያቄ ይጠቀማል ይህ አጋናኝ ጥያቄ በዐረፍተነገር መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ነገር ግን ከእኔ ጋር ወደ ኋላ ለመመለስ በልጆቼና በልጅ ልጆቼ ምንም ላደርግ አልችልም” (አግናኝ ጥቃቄዎች ይመልከቱ)

ምስክር ይሁን

እዚህ “ምስክር” የሚለው ቃል ሰውን አያመለክትም ነገር ግን ያዕቆብና ላባ የሚገቡትን ቃልኪዳን የሚያመለክትና በምሳለያዊነት የተጠቀመ ነው:: ምስክሩ ሁለቱ በሰላማዊ መንገድ ስስማሙ እንደተገኘ ሰው ተደርጐ ተነግሮአል (ሰውኛ አገላለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 31:45

ሐውልት

ይህ በክስተቱ ማብቂያ ያቆመው ትልቅ ድንጋይ ሲሆን አስፈላጊ ክስተት እንደተከናወነ ለማመለከት ነው

ድንጋይ ከመሩ

ድንጋዩን አንዱን በአንዱ ላይ በማድረግ ከመሩ

ከዚያም በድንጋዩ ክምር አጠገብ በሉ

አብሮ ምግብን መመገብ ቃል ኪዳን መፈጸሚያ አካል አንዱ ነው የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ይጋርሠሀዱታ

ተርጓሚዎች የማከተውን እንደግርጌ ማስናታወሻ ሊጠቀሙ ይችላሉ:: “ይጋርሠሀዱታ” የሚለው ስም በላባን ቋንቋ “ክምር ምስክርነት” ማለት ነው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ገለዓድ

ተርጓሚዎች የማከተውን እንደግርጌ ማስናታወሻ ሊጠቀሙ ይችላሉ:: “ገለዓድ” የሚለው ስም በላባን ቋንቋ “ክምር ምስክርነት” ማለት ነው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 31:48

ይህ ክምር በእኔና በአንተ መካከል ምስክር ነው

ድንጋዮች በእርግጥ እንደሰው ምስክር ሊሆኑ አይችሉም:: አት: “ይህ ክምር በእኔና በአንተ መካከል ማስታወሻ ይሆናል” (በሰውኛ አገላለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ገለዓድ

ተርጓሚዎች የማከተውን እንደግርጌ ማስናታወሻ ሊጠቀሙ ይችላሉ:: “ገለዓድ” የሚለው ስም በላባን ቋንቋ “ክምር ምስክርነት” ማለት ነው:: በዘፍጥረት 31:47 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ምጽጳ

ተርጓሚዎች የማከተውን እንደግርጌ ማስናታወሻ ሊጠቀሙ ይችላሉ:: “ምጽጳ” የሚለው “የመጠበቂያ ማማ” ማለት ነው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

እኛ በማንተያይበት ጊዜ

እዚህ “አለመተያየት” በተለያየን ይወክላል:: አት “በተለያየን ጊዜ” (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት ስለመጠቀም ይመልከቱ)

ማንም ከእኛ ጋር ባይኖር

እዚህ “እኛ” ያዕቆብንና ላባን ያመለክታል:: አት: “ማንም የሚያየን ባይኖር”

እይ

“ተመልከት” “አስተውል” “ለሚናገረው ነገር ትኩረት ስጥ”

Genesis 31:51

ይህ ክምር መሥክር ነው… ይህም ሐውልት ምሥክር ነው

የሰላም ስምምነታቸውን በሚመለከት እነዚህ የድንጋይ ክምሮች ለላባና ለያዕቆብ የማስታወሻና ድንበር ምልክቶች ናቸው:: እነዚህ እንደሰው ምሰክሮች እንደሆኑ ተደርጐ ተነግሮአል (በሰውኛ አገላለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

የአባቱ የይስሐቅ ፍርሃት

እዚህ “ፍርሃት” ይስሐቅ ለእግዚአብሔር ያለውን አክብሮትና ያንንም በመታዘዝ መግለጹን ያመለክታል፡፡

Genesis 31:54

ዘመዶቹንም ምግብ እንዲበሉ ጋበዛቸው

አብሮ ምግብ መብላት አብሮ ቃል ኪዳን የመግባት አካል ነው የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በማግስቱም ማለዳ…ወደ አገሩ ተመለሰ

ቁጥር 55 በመጀመሪያው የዕብራይስጡ መጽሐፍ የምዕራፍ 32 የመጀመሪያ ቁጥር ነው ነገር ግን በአብዛኛዎቹ ዘመናዊ መጽሐፍ ቅዱሶች የምዕራፍ 31 የመጨረሻ ቁጥር ነው በዘመናዊ መጽሐፍ ቅዱሶች የተጠቀመውን የቁጥር አቀማመጥ በቋንቋዎ እንዲጠቀሙ ይመከራል

የተባረከ

አዎንታዊና ጠቃሚ ነገሮች ለአንድ ሰው እንዲደረጉ መሻትን የሚገልጽ ማለት ነው


Chapter 32

1 ያዕቆብ በጉዞ ላይ ሳለ የእግዚአብሔር መላእክት በመንገድ ተገናኙት። 2 ባያቸውም ጊዜ፤ “ይህ የእግዚአብሔር ሰፈር ነው” አለ፤ የዚያንም ቦት ስም መሃናይም አለው። 3 ያዕቆብም በኤዶም አገር ሴይር በተባለው ምድር ወደሚኖረው ወንድሙ ወደ ዔሳው መልእክተኞችን አስቀድሞ ላከ፤ 4 እንዲህም ብሎ አዘዛቸው፤ “ጌታዬን ዔሳውን እንዲህ ትሉታላችሁ፤ ‘አገልጋይህ ያዕቆብ እንዲህ ብሎአል በሉት፤ ከላባ ዘንድ ተቀምጬ እስካሁን ድረስ እዚያው ኖርሁ፤ 5 ከብቶች፣ አህዮች፣ የበግና የፍየል መንጎች እንደዚሁም የወንድን የሴት አገልጋዮች አሉኝ፤ አሁንም ይህን መልእክት ለጌታዬ መላኬ በአንተ ዘንድ ሞግስ አገኛለሁ በሚል ተስፋ ነው።’” 6 የተላኩትም ሰዎች ወደ ያዕቆብ ተመልሰው፣ “ወደ ወንድምህ ወደ ዔሳው ሄደን ነበር፤ እርሱም ከአንት ጋር ለመገናኘት በመምጣት ላይ ነው፤ ከእርሱም ጋር አራት መቶ ሰዎች አሉ” አሉት። 7 በዚህ ጊዜ ያዕቆብ እጅግ በመፍራት ተጨነቀ፤ አብረውት የነበሩትንም ሰዎች በሁለት ክፍል መደባቸው፤ እንዲሁም በጎቹን፣ ፍየሎቹን፣ ከብቶቹንና ግመሎቹን በሁለት በሁለት መደባቸው። 8 ይህንንም ያደረገው፦ “ዔሳው የመጀመሪያውን ክፍል ቢያጠቃ፣ ሌላው ክፍል ሊያመልጥ ይችላል” ብሎ በማሰብ ነው። 9 ያዕቆብ እንዲህ ሲል ጸለየ፤ “የአባቴ የአብርሃም አምላክ፣ የአባቴ የይስሐቅ አምላክ ሆይ፣ ‘ወደ አገርህና ወደ ዘመዶችህ ተመልስ፣ እኔም በጎ ነገር አደርግልሃለሁ’ ያልኸኝ እግዚአብሔር ሆይ፣ 10 እኔ ባሪይህ እስካሁን ላደረግህልኝ ቸርነትና ታማኝነት ብቁ አይደለሁም፤ ዮርዳኖስን ስሻገር በእጄ ላይ ከነበረው በትር በስተቀር ምንም አልነበረኝም፤ አሁን ግን ይኸው ሁለት ሠራዊት ሆኛለሁ። 11 ከወንድሜ ከዔሳው እጅ እንድታድነኝ እለምንሃለሁ፤ መጥቶ እኔንም ሆነ እነዚህን እናቶች ከነልጆቻቸው ያጠፋናል ብዬ ፈርቻለሁኝ፤ 12 ነገር ግን አንተ ራስህ፣ ‘አበለጽግሃለሁ፤ ዘርህንም ሊቆጠር እንደማይችል እንደ ባሕር አሸዋ አበዛዋለሁ’ ብለኸኛል።” 13 በዚያችም ሌሊት ያዕቆብ እዚያው አደረ፤ ካለው ሀብት ለወንድሙ ለኤሳው እጅ መንሻ እንዲሆኑ እነዚህን መረጠ፦ 14 ሁለት መቶ እንስት ፍየሎችና ሃያ አውራ ፍየሎች፣ ሁለት መቶ እንስት በጎችና ሃያ አውራ በጎች፣ 15 ሠላሳ የሚያጠቡ ግመሎች ከነግልገሎቻቸው፣ አርባ ላሞችና ዐሥር ኮርማዎች፣ ሃያ እንስት አህዮችና ዐሥር ተባት አህዮች። 16 እነዚህንም በየመንጋው ለይቶ፣ የሚነዱአቸውን ጠባቂዎች መደበላቸው፤ ጠባቂዎችንም እናንተ ቀድማችሁ ሂዱ፣ መንጋዎቹንም አራርቃችሁ ንዱአቸው” አላቸው። 17 ቀድሞ የሚሄደውንም እንዲህ ሲል አዘዘው፤ ዔሳው አግኝቶህ ‘የማን ነህ? ወዴትስ ትሄዳለህ? የምትነዳውስ ይህ ሁሉ ከብት የማን ነው?’ ብሎ ቢጠይቅህ፣ 18 ‘የአገልጋይህ የያዕቆብ ናቸው፤ ለጌታዬ ለዔሳው እጅ መንሻ የሰደዳቸው ናቸው፤ እርሱም ከበስተኋላችን እየመጣ ነው’ ብለህ ንገረው 19 እንዲሁም ሁለተኛውን፣ ሦስተኛውንና መንጎቹን የሚነዱትን ሌሎቹንም ሁሉ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፤ ‘ዔሳውን ስታገኙት ይህንኑ ትነግሩታላችሁ፤ 20 በተጨማሪም ‘አገልጋይህ ያዕቆብ ከኋላችን እየመጣ ነው’ በሉት። ይህንንም ያዘዘው፣ ‘ዔሳው ከእኔ ጋር ከመገናኘቱ በፊት እጅ መንሻዬ አስቀድሞ ቢደርሰው ምናልባት ልቡ ይራራና በሰላም ይቀበለኛል’ ብሎ ስላሰበ ነበር። 21 ስለዚህ የያዕቆብ እጅ መንሻ ከእርሱ አስቀድሞ ተላከ፤ እርሱ ራሱ ግን እዚያው በሰፈሩ ቦታ አደረ። 22 በዚያኑ ሌሊት ያዕቆብ ተነሣ ሁለቱን ሚስቶቹን፣ ሁለቱን ሴት አገልጋዮቹንና ዐሥራ አንዱን ልጆቹን ይዞ የያቦቅን ወንዝ ተሻገረ። 23 ወንዙን አሻግሮ ከሸኛቸው በኋላ፣ ጓዙን ሁሉ ሰደደ። 24 ያዕቆብም ብቻውን እዚያ ቀረ፤ አንድ ሰውም እስኪነጋ ድረስ ሲታገለው አደረ። 25 ያም ሰው ያዕቆብን ታግሎ ማሸነፍ እንዳቃተው በተረዳ ጊዜ፣ የጭኑን ሹልዳ መታው፣ ያዕቆብም በሚታገልበት ጊዜ ጭኑ ከመገጣጠሚያው ላይ ተለያየ፤ 26 በዚያን ጊዜ ሰውዬው፣ “እንግዲህ መንጋቱ ስለሆን ልቀቀኝና ልሂድ” አለው። ያዕቆብም፣ “ካልባረክኸኝ አልለቅህም” አለው። 27 ሰውዬውም፣ “ስምህ ማን ነው?” አለው። እርሱም፣ “ያዕቆብ ነው” አለ። 28 ሰውዬውም፣ “ከእግዚአብሔርም ከሰዎችም ጋር ታግለህ አሸንፈሃልና ከእንግዲህ ስምህ እስራኤል እንጂ ያዕቆብ አይባልም” አለው። 29 ያዕቆብም፣ “እባክህ ስምህን ንገረኝ” ብሎ ጠየቀው። ሰውዬውም፣ “ስሜን ለማወቅ ለምን ፈለግህ?” አለው፤ በዚያም ስፍራ ባረከው። 30 ስለዚህ ያዕቆብ “እግዚአብሔርን ፊት ለፊት ዐይቼ እንኳ ሕይወቴ ተርፋለች” ሲል የዚያን ቦታ ስም ጵኒኤል አለው። 31 ጵኒኤልንም እንዳለፈ ፀሐይ ወጣችበት፣ እርሱም በጭኑ ምክንያት ያነክስ ነበር። 32 ከዚህም የተነሣ የእስራኤል ልጆች ሹልዳን ከጭኑ ጋር የሚያገናኘውን ሥጋ አይበሉም፤ ምክንያቱም ያዕቆብ ከሰውዬው ጋር ሲታገል ሰውዬው ሹልዳውን መትቶት ስለነበር ነው።



Genesis 32:1

መሃናይም

ተርጓሚዎች በግርጌ ማስታወሻዎች ሊጨምሩ ይችላሉ:: መሃናይም የሚለው ስም “ሁለት ሰፈሮች” ማለት ነው

Genesis 32:3

ሴይር

ይህ በኤዶምያስ ግዛት ተራራማው ቦታ ነው:: ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ::

ጌታዬን ዔሣውን እንዲህ ትሉታላችሁ “አገልጋይህ ያዕቆብ እንዲህ ብሎአል በሉት “እስካሁን …. በፊትህ’”

ይህ በጥቅስ ውስጥ የሚገኝ ጥቅስ አለው:: ቀጥታው ጥቅስ እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ ‘ይህ ለጌታዬ ለዔሣው ሊነግር የሚወደው ነው:: እስከዚህ እንዳለሁት ……በፊቱ’” (ጥቅስን በጥቅስ ውቅጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ጌታዬ ዔሣው

ያዕቆብ ወንድሙን ጌታው አድርጐ በማቅረብ የትህትና ቃል ይጠቀማል

አገልጋይህ ያዕቆብ

ያዕቆብ ራሱን እንደአገልጋዩ በማድረግ የትህትና ቃል ይጠቀማል

በአንተ ፊት ሞገስ ባገኝ

ሞገስ ማግኘት የሚለው ሀረግ በሌሎች ሰዎች ዘንድ ተቀባይነትን ማትረፍን የሚገልጽ ፈሊጣዊ አባባል ነው አት “መቀበልህን እንዲታረጋግጥልኝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ተመሣሣይ ምትክ ቃላትና ዘይቤያዊ አባባሎች ይመልከቱ)

Genesis 32:6

አራት መቶ ሰዎች

4ዐዐ ሰዎች ቁጥሮች ይመልከቱ

ፍርሃት

አንድ ሰው በራሱ ወይም ከሌሎች ሥጋት የሚፈጥር ጉዳት ሲደረስበት የማሰማው ስሜት ነው

ጭንቀት

ተስፋ መቁረጥ ወይም መረበሽ

በአንደኛው ሠፈር ላይ አደጋ ቢጥል ሌላው ሠፈር ሊያመልጥ ይችላል

እዚህ ሠፈር ሰዎችን ይወክላል አት በአንዱ ሠፈር ባለው ሰው አደጋ ቢጣል በሌላው ሠፈር ያለው ሰው ያመልጣል፡፡ (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 32:9

የአባቴ የአብርሃም አምላክ የአባቴ የይስሐቅ አምላክ ሆይ

ይህ ለተላያዩ አማልክት ሳይሆን ሁሉም ያመለኩትን አንድ እግዚአብሔርን ያመለክታል አት የአያተ የአብርሃምና የአባተ የይስሐቅ አምላክ እግዚአብሔር (ግምታዊ እውቀትና ጥብቅ መረጃ ይመልከቱ)

ወደ አገርህና ወደ ዘመዶችህ ተመለስ እኔም በጐ ነገርን አደርግልሃለሁ ያልከኝ እግዚአብሔር ሆይ

ይህ በጥቅ ውስጥ የሚገኝ ጥቅሰ ነው:: በተዘዋዋሪ ጥቅስ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ወደ አገረና ወደ ሕዝቤ እንድመለስና በጐ ነገርንም አደርግልሃለሁ ያልከው እግዚአብሔር”

ወደ ዘመዶችህ

ወደ ቤተሰብህ

በጐ ነገር አደርግልሃለሁ

መልካም ነገር አደርግልሃለሁ ወይም በመልካምነት እንከባከብሃለሁ

እኔ ባሪያህ እስካሁን ላደረክልኝ የቃልኪዳን ቸርነትና ታማኝነት ብቁ አይደለሁም

ረቂቅ ስሞች ቸርነትና ታማኝነት እንደ ቸር እና ታዛዥ ሊገለጹ ይችላሉ አት እኔ ባሪያህ እስካሁን ላደረክልኝ የቃልኪዳን ታማኝ አይደለሁም ወይም ታዛዥ አይደለሁም (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተነገር ይመልከቱ)

ባሪያህ

“እኔ” የሚለው በትህትና ቃል ሲገለጽ ነው

አሁን ግን የሁለት ክፍል ሠራዊት ሆንሁ

ሆንሁ የሚለው ሐረግ ያለውን ሀብት የሚገልጽ ፈሊጣዊ አባባል ነው:: አት: “አሁን ግን ከእኔ ጋር በሁለት ክፍል ሠራዊት በቂ ሰዎች መንጋዎችና ሀብት አሉኝ” ፈሊጣዊ አባባል ይመልከቱ

Genesis 32:11

አድነኝ

አትርፈኝ

ከወንድሜ እጅ ከዔሣው እጅ

እዚህ “እጅ” ጉልበትን ያመለክታል ሁለቱም ሀረጐች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው ሁለተኛው የሚገልጸው ያዕቆብ የሚያስበው ወንድመ ዔሣው እንደሆነ ነው፡፡ አት፡ ከወንድሜ ከዔሣው ጉልበት ወይም ከወንድሜ ከዔሣው (ተመሣሣይ ምትክ ቃል ወይም ተጓዳኝ ንጽጽር ይመልከቱ)

እንዳያጠፋ እኔ እፈራለሁና

እንደሚያጠፋ ፈርቼያለሁና

ነገር ግን አንተ ራስህ አበለጽግሃለሁ ዘርህን ሊቈጠር….

ይህ በጥቅስ ውስጥ ያለ ጥቅስ ነው እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ነገር ግን አንተ ራስህ አብለጽግሃለሁ እናም የዘረንም ቁጥር..” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና በዘዋዋሪ ጥቅችን ይመልከቱ)

አበለጽግሃለሁ

መልካም ነገርን አደርግልሃለሁ ወይም በመልካምነቴ አሳይሃለሁ

ዘርህን እንደ ባህር አሸዋ አበዛዋለሁ

የያዕቆብን ዘር ቁጥር እጅግ ብዙ ማድረጉ ቁጥሩ እንደ ባህር አሸዋ ቁጥር እንደሚሆን ተደርጐ ተነግሮአል (ተመሣሣይ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ሊቆጠር እንደማይችል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት: “ያም ከቁጥራቸው የተነሣ ማንም መቁጠር እስከማይችል” (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 32:13

ሁለት መቶ

2ዐዐ (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ሃያ …. ሠላሣ …. አርባ … አሥር

20 …. 30 …. 40 ….10 (ቁጥሮች ይመልከቱ)

ግልገሎች

እየጠቡ ያሉ ለጋ እንስሳት

እነዚህንም መንጐች በየወገኑ ከፍሎ በባሪያዎች እጅ አደረጋቸው

እዚህ “በእነሱ እጅ” በእነሱ ቁጥጥር ሥር አደረገ ማለት ነው:: አት በየወገኑ ከፈላቸው እናም እያንዳንዱን መንጋ በእያንዳንዱ ባሪያ ቁጥጥር ሥር አደረገ (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

መንጋውንና መንጋውን አራርቁት

አንዱ መንጋ ከሌላው መንጋ በርቀት እንዲጓዝ አድረጉ

Genesis 32:17

መመሪያ ሰጠው

አዘዘው

በፊትህ ያለው… የማን ነው? ብሎ የጠየቀህ እነደሆነ

ይህ በጥቅስ ውስጥ ያለ ጥቅስ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “የማን ነህ? ወዴትስ ተሄዳለህ? የምትነዳውስ ይህ ሁሉ ከብት የማን ነው? ብሎ ቢጠይቅህ” (ጥቅስ በጥቅስ ውስጥ እና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶች ይመልከቱ)

የማን ነህ?

ጌታህ ማን ነው?

በፊትህ ያለው ይህ ሁሉ ከብት የማን ነው?

በፊትህ ያለው የዚህ ሁለ ከብት ባለቤት ማን ነው?

በዚያን ጊዜ አንተ ለጌታዬ ለዔሣው እጅ መንሻ የሰደደው የባሪያህ የያዕቆብ ነው እርሱም ደግሞ ከኋላችን እየመጣ ነው፤ በለው

ይህ በጥቅስ ውስጥ የሚገኝ ጥቅስ ነው በተዘዋዋሪ ጥቅስ መልክ ሊገለጽ ይችላል፤ አት፤ “በዚያን ጊዜ እነዚህ ሁሉ የአገልጋይህ የያዕቆብ ናቸው፤ ለጌታዬ ለዔሣው እጅ መንሻ የሰደዳቸው ናቸው፤ እርሱም ሊገናኝህ ከበስተኋላችን እየመጣ ነው፤ ብለህ እንዲትነግረው እፈልጋለሁ::” (ጥቅስ በጥቅስ ውስጥ እና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶች ይመልከቱ)

የአገልጋይህ የያዕቆብ ናቸው

የዕቆብ ራሱን ትህትናን በተሞላ መንገድ የዔሣው ባሪያ አድርጐ ያቀርባል

ለጌታዬ ለዔሣው

ያዕቆብ በትህትና ዔሣውን እንደ ጌታው መቁጠሩን ያመለክታል

ከእኛ ኋላችን እየመጣ ነው

እኛ የሚናገረውን ባሪያ ያመለክታል እናም ሌሎች ባሪያዎችም ለዔሣው እጅ መንሻ ይዘው እየመጡ እንዳለ ይገለጻል (ብዙና ነጠላ “እኛ” ይመልከቱ)

Genesis 32:19

ለሁለተኛው ቡድን መመሪያ ሰጠ

ሁለተኛውን ቡድን አዘዘ

ይህኑን ትነግሩታላችሁ ባሪያህ ያዕቆብ

አማራጭ ተገቢ ትርጉሞች 1) “ደግሞም እንዲህ ትነግሩታላችሁ ባሪያህ ያዕቆብ” 2) “ደግሞም እንዲህ ትላላችሁ ባሪያህ ያዕቆብ”

አስደስት ይሆናል

አረጋጋው ይሆናል ወይም ቁጣው እንዲርቅ አደርግ ይሆናል

ይቀበለኛል

በርኀራኄ ይቀበለኛል

የያዕቆብ እጅ መንሻ ከእርሱ አስቀድሞ ተላከ

እዚህ እጅ መንሻ እጅ መንሻውን ይዘው የሄዱ ባሪያዎች ይወክላል (ምትክ አባባሎችን የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

እርሱ ራሱ ግን እዚያው አደረ

እዚህ “ራሱ” ያዕቆብ ከባሪያዎቹ ጋር እንዳለሄደ አበክሮ ይናገራል (ተጣቃሽ ተውላጤ ስም ይመልከቱ)

Genesis 32:22

ሁለት ሴት ባሪያዎቹ/አገልጋዮቹ

ሁለት ባሪያ/አገልጋይ ሚስቶቹ፤ ዘለፋና ባላ ማለት ነው

የወንዝ መልካ

በወንዝ ጥልቅ ያልሆነ በቀላሉ የሚያሻግር ቦታ

ያቦቅ

ይህ የወንዝ ስም ነው ስሞችን እንዴት እንደሚተረጉሙ ይመልከቱ

ንብረቱን ሁሉ

ያለውን ነገር ሁሉ

Genesis 32:24

እስኪነጋ

ንጋት ድረስ

የጭኑ ሹልዳ ሲታገለው ደነዘዘ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ልገለጽ ይችላል፤ አት: “በሚታገልበት ጊዜ የሚታገለው ሰው የያዕቆብን ሹልዳ ጐዳው” (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ጭን

ከዳሌ ጋር የተያያዘ ላይኛው የእግር አካል ነው

ሊነጋ ሲል

ጸሐይ ከመውጣትዋ በፊት

መባረክ

በአንድ ሰው ላይ በረከትን ማዘዝና ለዚያ ሰው መልካም ነገር እንዲሆኑለት ማድረግ ነው

ካልባረክሄኝ አልለቅህም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ልገለጽ ይችላል፤ አት: “በእርግጥ አልለቅህም መጀመሪያ ባርከኝና ከዚያም እለቅሃለሁ” (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ) (ድርብ አሉታዊ አባባሎች ይመልከቱ)

Genesis 32:27

እስራኤል

ተርጓሚዎች የግርጌ መስታወሻ እንደሚከተለው ሊጨምሩ ይችላሉ እስራኤል የሚለው ስም ከእግዚአብሔር ጋር ይታገላል ማለት ነው ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ

ሰዎች

ሰዎችን በገሃድ የሚገልጽ ነው

Genesis 32:29

እርሱም ስሜን ለምን ትጠይቃለህ? አለው

እርሱም ስለ ስሜ ለምን ተቀጠይቃለህ አለው ይህ አግናኝ ጥያቄ ያዕቆብን የሚያደነግጠው የሚገሥጸውና በእርሱና ከእርሱ ጋር ሲታገል በቆየው ሰው መካከል ምን እንደተከሰተ እንዲያስብ የሚያደርገው ነው:: አት: “ስሜን አትጠይቅ” (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ጵንኤል

ተርጓሚዎች የግርጌ መስታወሻ እንደሚከተለው ሊጨምሩ ይችላሉ:: “ጵንኤል” የሚለው ስም “የእግዚአብሔር ፊት” ማለት ነው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)፡፡

ፊት ለፊት

“ፊት ለፊት” ሁለት ሰዎች በቅርበት በአካል የሚተያዩበት ማለት ነው::

ሕይወቴ ተርፋለች

ይህ በሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት ሕይወቴን አትርፎአታል:: (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 32:31

ከዚህም የተነሣ እስከ ዛሬ ድረስ

ይህ ታሪኩ ወደ እስራኤል ዘር ዳራ ትረካ እንተለወጠ አመላካች ነው (የዳራ መረጃ ይመልከቱ)

የጭኑ ሹልዳ

ሹልዳን ከጭኑ ጋር የሚያገናኝ የጡንቻ ሥጋ ያመለክታል

ተነክቶ ነበር

ሲታገል ተነክቶ ነበር


Chapter 33

1 ያዕቆብ አሻግሮ ተመለከተ፤ እነሆ፣ ዔሳው አራት መቶ ሰዎች አስከትሎ እየመጣ ነበር። ስለዚህ ያዕቆብ ልጆቹን ለልያ ለራሔልና ለሁለቱ አገልጋዮቹ አከፋፈላቸው። 2 ከዚያም ሁለቱን አገልጋዮች ከነልጆቻቸው አስቀደመ፤ ልያንና ልጆቿንም አስከተለ፤ ራሔልንና ዮሴፍን ግን ከሁሉ ኋላ እንዲሆኑ አደረገ። 3 እርሱ ራሱም ቀድሞአቸው ሄደ፤ ወንድሙም ዘንድ እስኪደርስ ድረስ ሰባት ጊዜ ወደ መሬት ለጥ ብሎ እጅ ነሣ። 4 ዔሳው ግን ሊገናኘው ወደ እርሱ ሮጦ ሄዶ አቀፈው፤ በአንገቱም ላይ ተጠምጥሞ ሳመው፤ ሁለቱም ተላቀሱ። 5 ከዚያም ዔሳው ቀና ብሎ ሲመለከት ሴቶቹንና ልጆቹን ዐየ፤ እርሱም፣ “እነዚህ አብረውህ ያሉ እነማን ናቸው?” ብሎ ጠየቀው። ያዕቆብም መልሶ፣ “እነዚህማ እግዚአብሔር በቸርነቱ ለእኔ ለአገልጋይህ የሰጠኝ ልጆች ናቸው” አለው። 6 በዚህ ጊዜ ሁለቱ ሴት አገልጋዮችና ልጆቻቸው ቀርበው እጅ ነሡ፤ 7 ከዚያም ልያና ልጆቿ መጥተው እጅ ነሡ፤ በመጨረሻም ዮሴፍና ራሔል መጡ፤ እነርሱም ቀርበው እጅ ነሡ። 8 ዔሳውም፣ “ወደ እኔ ተነድቶ የመጣው ይህ ሁሉ መንጋ ምንድነው?” አለው። ያዕቆብም፣ “ጌታዬ ሆይ፣ በአንተ ዘንድ ሞገስ ባገኝ ብዬ ነው” አለው። 9 ዔሳው ግን፣ “ወንድሜ ሆይ፤ እኔ በቂ አለኝ፤ የራስህን ለራስህ አድርገው” አለው። 10 ያዕቆብም፣ “የለም፣ እንዲህ አይደለም፤ በአንተ ዘንድ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ፣ እጅ መንሻዬን ተቀበል፤ በመልካም ሁኔታ ተቀብለኸኝ ፊትህን ማየት መቻሌ ራሱ፣ የእግዚአብሔርን ፊት የማየት ያህል እቆጥረዋለሁ። 11 እግዚአብሔር በቸርነቱ አሟልቶ ስለ ሰጠኝ የሚያስፈልገኝ ሁሉ አለኝና ያቀረብሁልህን እጅ መንሻ እባክህ ተቀበለኝ” አለው። ያዕቆብ አጥብቆ ስለለመነው፣ ዔሳው እጅ መንሻውን ተቀበለ። 12 ዔሳውም፣ “እንግዲህ እንሂድ፤ እኔም ከአንተ ቀድሜ እሄዳለሁ” አለው። 13 ያዕቆብ ግን እንዲህ አለው፤ “ጌታዬ እንደምታየው ልጆቹ ይህን ያህል የጠኑ አይደሉም፣ ለሚያጠቡት በጎችና ጥገቶች እንክብካቤ ማድረግ አለብኝ፤ እንስሳቱ ለአንዲት ቀን እንኳ በጥድፊያ ቢነዱ በሙሉ ያልቃሉ። 14 ስለዚህ ጌታዬ፣ አንተ ቀድመኸኝ ሂድ፤ እኔም በምነዳቸው እንስሳትና በልጆቹ ጉዞ አቅም ልክ እያዘገምሁ ሴይር ላይ እንገናኛለን” 15 ዔሳው፣ “እንግዲያስ ከሰዎቼ ጥቂቶቹን ልተውልህ” አለው። ያዕቆብ ግን፣ “ለምን ብለህ? በአንተ ዘንድ ሞገስ ማግኘቴ ይበቃኛል” አለው። 16 ስለዚህ ዔሳው በዚሁ ዕለት ወደ ሴይር ለመመለስ ተነሣ። 17 ያዕቆብ ግን ወደ ሱኮት ሄደ፤ እዚያም ለራሱ መጠለያ፣ ለከብቶቹም በረት ሠራ፤ ከዚህም የተነሣ የቦታው ስም ሱኮት ተባለ። 18 ያዕቆብ ከመስጴጦምያ በተመለሰ ጊዜ በከነዓን ምድር ወዳለችው ወደ ሴኬም በሰላም ደረሰ፤ በከተማይቱም ፊት ለፊት ሰፈረ። 19 ድንኳኑን የተከለበትንም ቦታ የሴኬም አባት ከነበረው ከኤሞር በመቶ ጥሬ ብር ገዛው፤ 20 በዚያም መሠዊያ አቁሞ፤ ኤል ኤሎሄ እስራኤል ብሎ ጠራው።



Genesis 33:1

እነሆ

“እነሆ” የሚለው ቃል ለሚያስደንቀው ለታሪኩ አድስ ክፍል ትኩረት እንዲንስጥ ያደርጋል

አራት መቶ ሰዎች

400 ሰዎች (ቁጥሮች ይመልከቱ)

ያዕቆብ ልጆቹን ….. ለሴት አገልጋዮች አከፋፈላቸው

ይህ እያንዳንዷ ሴት ተመሣሣይ ቁጥር ልጆች እንዲኖራት ያዕቆብ ልጆቹን አከፈላቸው ማለት አይደለም እያንዳንዱ ልጅ ከእናቱ ወይም ከእናትዋ ጋር የሆን ዘንድ ያዕቆብ ለጆቹን አከፋፈላቸው (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሴት አገልጋዮች

“አገልጋይ ሚስቶች” ዘለፋንና ባላን ያመለክታል

እርሱ ራሱ ቀድሞአቸው ሄደ

እዚህ ራሱ የሚለው ያዕቆብ ራሱ በሌሎች ፊት ቀድሞ እንደሄደ ትኩረት ይሰጣል (ተጣቃሽ ተውላጤ ስም ይመልከቱ)

ጐንበስ ብሎ እጅ ነሣ

ጐንበስ ማለት አንድን ሰው በትህትና መቀበልንና ማክበርን ይገልጻል (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Genesis 33:4

ሊገናኘው

ያዕቆብን ሊገናኝ

ዐቀፈው በአንገቱም ላይ ተጠምጥሞ ሳመው

ይህ እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ዔሣው በያዕቆብ ላይ እጆቹን ጠምጥሞ አቀፈው እናም ሳመው”

ከዚያም ሁለቱ አለቀሱ

ይህ በግልጽ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ከዚያም እንደገና በመተያየታቸው ተደስተው ዔሣው ያዕቆብ አለቀሱ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሴቶቹንና ልጆቹን አየ

ከያዕቆብ ጋር ያሉ ሴቶቹንና ልጆቹን አየ

እነዚህማ እግዚአብሔር በቸርነቱ ለእኔ ለአገልጋይህ የሰጠኝ ልጆች ናቸው

የአንተ አገልጋይ የሚለው ሀረግ ያዕቆብ ራሱን በትህትና ያቀረበው መንገድ ነው:: አት: “እነዚህ እግዚአብሔር በቸርነቱ ለአገልጋይህ የሰጠኝ ልጆች ናቸው” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 33:6

አገልጋይ ሴቶች

ሴት አገልጋዮች፡፡ ባላንና ዘለፋን ያመለክታል፡፡

ጐንበስ አለ

በሌላ ሰው ፊት ትህትናንና አክብሮትን የሚያሳይ ምልክት ነው:: (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

ወደ እኔ ተነድቶ የመጣው ይህ ሁሉ መንጋ ምንድን ነው?

“ይህ ሁሉ” የሚለው ሀረግ ያዕቆብ በየቡድኑ በባሪያዎች ለዔሣው የላከውን ስጦታዎች ያመለክታል:: አት: “እነኛ የተለያዩ ቡድኖች ሁሉ እንዲገናኙኝ ለምን ላክሃቸው?”

በጌታዬ ፊት ሞገስ ባገኝ ብዬ ነው

ሞገስ ማግኘት የሚለው ሀረግ በአንድ ሰው ተቀባይነትን ማረጋገጥ የሚል ትረጉም የያዘ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው እንዲሁም ደግሞ ፊት ፍርድን ወይም ግማገማን ይወክላል አት አንተ ጌታዬ እንዲትደሰትብኝ ነው (ፈሊጣዊና ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ጌታዬ

ጌታዬ ዔሣው በትህት መንገድ ዔሣው የተገለጸበት ነው:: (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 33:9

እኔ በቂ አለኝ

እንስሳት ወይም ንብረት የታወቁ ቃላት ናቸው:: አት: “በቂ እንስሳት አለኝ ወይም በቂ ንብረት አለኝ” (ድብቅ አገላለጽ ይመልከቱ)

በአንተ ዘንድ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ

ሞገስ ማግኘት የሚለው ሀረግ በአንድ ሰው ተቀባይነትን ሰለማኘት የሚገልጽ ፈሊጣዊ አባባል ነው እዚህ ዓይን የማየት ምትክ ቃል ሲሆን ማየት ግምገማውን የሚገልጽ ዘይቤያዊ አነጋገር ነው:: አት: “በእኔ የተደሰትህ እንደሆነ” (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የሊጣዊና ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እጅ መንሻዬ

“እጅ” ያዕቆብን ያመለክታል አት ይህ ለአንተ የሚሰጠው እጅ መንሻዬ ነው (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በውኑ እጅ መንሻዬ

እንደ አድስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “በእርግጥም እጅ መንሻዬ”

የእግዚአብሔርን ፊት እንደሚያይ ፊትህን አይቼአለሁና

ይህ ተመሣሣይ አባባል ግልጽ አይደለም ተገቢ ትርጉሞች የሚከተሉት ናቸው 1 እግዚአብሔር ይቅር እንዳለለት ዔሣውም ይቅር እንዳለው ያዕቆብ ደስተኛ ነው ወይም 2 ያዕቆብ እግዚአብሔርን በመገናኘቱ እንደተደነቀው ሁሉ ዔሳውን በመገናኘቱ ተደንቆአል 3 ያዕቆብ በእግዚአብሔር መገኘት ራሱን እንዳዋረደው ሁሉ በዔሣው ፊት ራሱን ያዋርዳል (ተመሣሣይ አባባሎችን ይመልከቱ)

ፊትህን አይቻለሁ

እዚህ ፊት ዔሣውን ያመለክታል ይህ ፊት በመባል ሊተረጐም ይችላል፤ ምክንያቱም “ፊት” የሚለው ቃል በዘፍጥረት 32:3ዐ “የእግዚአብሔር ፊት” እና “ፊት ለፊት” ለመግለጽ ተጠቅሞአል (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ይህችንም ያመጣሁልህ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ይህም አገልጋዮቼ ያመጡልህ” (ተሻጋሪና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እግዚአብሔር በቸርነቱ አሟልቶ ስለሰጠኝ

እግዚአብሔር በቸርነቱ ስለመለከተኝ ወይም እግዚአብሔር እጅግ በጣም ስለባረከኝ

ያዕቆብም አጥብቆ ስለለመነው ዔሣው እጅ መንሻውን ተቀበለ

አንድን ሥጦታ ላለመቀበል መገዳደር ነገር ግን ከዚያ በኋላ ሰጪው እንዳያዝን መቀበል የተለመደ ባህላዊ መንገድ ነው

Genesis 33:12

ጌታዬ ያውቃል

ይህ በትህትናና በመደበኛ መንገድ ዔሣውን ማመልከት ነው:: አት: “አንተ ጌታዬ ታውቃለህ” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ልጆች የጠኑ አይደሉም

ትርጉሙም ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ አት፡ “በፍጥነት ለመጓዝ ልጆች ገና የጠኑ አይደሉም”:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይጠቀሙ)

አንዲት ቀን እንኳ በጥድፍያ ቢነዱ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ለአንድ ቀን እንኳ በፍጥነት እንዲጓዙ ቢናጣድፋቸው” (ተሻጋሪና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ጌታዬ ከባሪያው ቀድሞ ይሂድ

ይህ ያዕቆብ ራሱን በመደበኛና በትህትና መንገድ የሚገልጸው ነው:: አት: “ጌታዬ እኔ ባሪያህ ነኝ” (ከፊቴ ቀድመህ ሂድ አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

በሚነዱአቸው እንስሳት እርምጃ ልክ

“በሚነዱአቸው እንስባት እርምጃ ፍጥነት መጠን”

ሴይር

በኤዶም ግዛት የሚገኝ ተራራማ ሥፍራ ነው፡፡ በዘፍጥረት 32 3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

Genesis 33:15

ለምንድር ነው?

ዔሣው ሰዎቹን መተው እንደሌለበት ለማጽናት ያዕቆብ ጥያቄን ይጠቀማል:: አት: “ይህን አታድርገው” ወይም “ይህን ማድረግ አይገባህም” (አግናኝ ጥያቄዎች ይመልከቱ)

ጌታዬ

ይህ በመደበኛና በትህትና ዔሣውን የሚግለጽ ነው:: አት: “አንተ ጌታዬ” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ሱኮት

ተርጓሚዎች እንደግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ ሱኮት የሚለው ስም መጠለያዎች ማለት ነው ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ

ለራሱ ቤትን ወይም መጠለያን ሠራ

ይህ የተሠራው ቤት ለቤተሰቡም እንደሆነ ያመለክታል፡፡ አት፡ “ለራሱና ለቤተሰቡ ቤት ሠራ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ለመንጋው

ለሚጠብቁአቸው እንስሳት

Genesis 33:18

አጠቃላይ መረጃ

ይህ አድስ የታሪኩን አካል ይጀምራል በሱኮት ካረፈ በኋላ ያዕቆብ ምን እንዳደረገ ጸሓፊው ይገልጻል

ያዕቆብ ወደ ጳዳን አራም በመጣ ጊዜ

ያዕቆብ ….. ደረሰ ….. ሠፈረ

ይህ ያዕቆብ የቤሰቡ መሪ ስለሆነ እርሱን ብቻ ይጠቅሳል::

የእርሱም ቤተሰብ ከእርሱ ጋር እንደነበር ግልጽ ነው (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አጠገብ ሠፈረ

በቅርበት ሠፈረ

ከፊል መሬት

ከፊል ቦታ

ኤሞር

የአንድ ሰው ስም ነው

የሴኬም አባት

ሴኬም የሰውዬውና የከተማይቱ ስም ነው

አንድ መቶ

1ዐዐ (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ኤል ኤሎሄ እስራኤል

ተርጓሚዎች የግርጌ ማስታወሻ እንደሚከተለው ሊጨምሩ ይችላሉ አት ኤል ኤሎሄ የሚለው ቃል እግዚአብሔር የእስራኤል አምላክ ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)


Chapter 34

1 ልያ ለያዕቆብ የወለደችለት ሴት ልጅ ዲና፤ አንድ ቀን የዚያን አገር ሴቶች ለማየት ወጣች። 2 የአገሩ ገዥ የኤዊያዊ የኤሞር ልጅ ሴኬም ባያት ጊዜ ያዛት በማስገደድም ክብረ ንጽሕናዋን ደፈረ። 3 ልቡ በያዕቆብ ልጅ በዲና ተማረከ፤ ልጅቷንም በጣም ወደዳት፤ በጣፈጠም አንደበት አናገራት። 4 ሴኬምም አባቱን ኤሞርን፣ “ይህችን ልጅ አጋባኝ” አለው። 5 ያዕቆብ የልጁን የዲናን ክብረ-ንጽሕና ሴኬም እንደደፈረ ሰማ፤ ነገር ግን ወንዶች ልጆቹ የከብት መንጋ ይዘው ተሰማርተው ስለነበር፣ እነርሱ እስኪመጡ ዝም ብሎ ቆየ፤ 6 ከዚያም የሴኬም አባት ኤሞር፣ ያዕቆብን ሊያነጋግረው ወጣ። 7 የያዕቆብ ወንዶች ልጆችም የተፈጸመውን ድርጊት እንደሰሙ ወዲያውኑ ከመስክ መጡ፤ ሴኬም መደረግ የማይገባውን አስነዋሪ ነገር በእስራኤል ላይ በመፈጸም የያዕቆብን ልጅ ስለደፈረ አዘኑ እጅግም ተቆጡ። 8 ኤሞር ግን እንዲህ አላቸው፤ “ልጄ ሴኬም ልጃችሁን በጣም ወዶአታል፤ ስለዚህ እንዲያገባት ፍቀዱለት፤ 9 በጋብቻ እንተሳሰር፣ ሴት ልጃችህን ስጡን፣ የእኛንም ሴቶች አግቡ። 10 አብራችሁንም መኖት ትችላላችሁ፤ አገራችን አገራችሁ ናት፣ ኑሩባት፤ ነግዱባት፣ ሀብት ንብረትም አፍሩባት። 11 ሴኬም ደግሞ የዲናን አባትን ወንድሞች እንዲህ አላቸው። “በእናንተ ዘንድ ሞገስ ላግኝ እንጂ የተጠየቅሁትን ሁሉ እሰጣለሁ፤ 12 ለሙሽራዋም ጥሎሽ የፈለጋችሁትን ያህል ጠይቁኝ፤ እርሷን እንዳገባ ፍቀዱልኝ እንጂ፣ የፈለጋችሁትን ሁሉ ለመጠት ዝግጁ ነኝ።” 13 ሴኬም እኅታቸውን ዲናን አስነውሮ ስለነበር የያዕቆብ ልጆች ለእርሱና ለአባቱ በተንኮል እንዲህ ሲሉ መለሱላቸው፣ 14 እንዲህ አሉአቸው፤ “እኅታችንን ላልተገረዘ ሰው ብንሰጥ ውርደት ስለሚሆንብን፣ እንዲህ ያለውን ነገር አናደርገውም። 15 ሆኖም የምንስማማበት አንድ መንገድ ብቻ አለ፤ ይኸውም አንተና በእናንተ ዘንድ ያሉት ወንዶች ሁሉ እንደኛ የተገረዛችሁ እንደሆነ ነው። 16 እንዲህ ከሆነ እናንተ የእኛን ሴቶች ልጆች ታገባላችሁ፣ እኛም የእናንተን ሴቶች ልጆች እናገባለን፣ አንድ ሕዝብ ሆነንም አብረን እንኖራለን። 17 ዐሳባችንን ባትቀበሉና ባትገረዙ ግን እኅታችንን ይዘን እንሄዳለን። 18 ያቀረቡትም ዐሳብ ለኤሞርና ለልጁ ለሴኬም መልካም መስሎ ታያቸው። 19 ከአባቱ ቤተሰብ ሁሉ እጅግ የተከበረው ይህ ወጣት የያዕቆብን ልጅ እጅግ ወዶአት ስለነበር፣ ያሉትን ለማድረግ ጊዜ አልወሰደበትም። 20 ስለዚህ ኤሞርና ልጁ ሴኬም ይህንኑ ለወገኖቻቸው ለመንገር ወደ ከተማቸው በር ሄዱ፤ 21 እንዲህም አሏቸው፤ “እነዚህ ሰዎች ከእኛ ጋር የሚኖሩት በሰላም ነው፣ በምድሪቱ ላይ አብረው ይቀመጡ፣ ተዘዋውረውም እንዲነግዱ እንፍቀድላቸው፤ ምድሪቱ እንደሆን ለእኛም ለእነርሱም ትበቃለች። ሴቶች ልጆቻቸውን እናገባለን፤ እነርሱም የእኛን ሴቶች ልጆች ያገባሉ፤ 22 ሆኖም ሰዎቹ ከእኛ ጋር እንደ አንድ ሕዝብ ሆነው አብረውን ለምኖር ፈቃደኞች የሚሆኑት፣ የእኛ ወንዶች እንደ እነርሱ የተገረዙ እንደሆነ ብቻ ነው። 23 ታዲያ እንዲህ ብናደርግ ከብታቸው ንብረታቸው፣ እንስሶቻቸውም ሁሉ የእኛው ይሆኑ የለምን? ስለዚህ ባሉት እንስማማ፣ እነርሱም አብረውን ይኑሩ።” 24 የከተማይቱ ነዋሪዎች ሁሉ ኤሞርና ሴኬም ባቀረቡት ዐሳብ ተስማምተው ወንዶቹ ሁሉ ተገረዙ። 25 በሦስተኛውም ቀን የሁሉም ቁስል ገና ትኩስ ሳለ ከያዕቆብ ልጆች ሁለቱ፣ የዲና ወንድሞች ስምዓንና ሌዊ፣ ሰይፋቸውን መዘው ሳይታሰብ ወደ ከተማይቱ ገብተው ወንዶቹን በሙሉ ገደሏቸው። 26 ኤሞርንና ሴኬምንም በሰይፍ ገድለው፣ እኅታቸውን ዲናን ከሴኬም ቤት አውጥተው ይዘዋት ተመለሱ። 27 የቀሩትም የያዕቆብ ልጆች እኅታቸውን ስለደፈሩባቸው ወደ ሞቱት ሰዎች ቤት እየገቡ ከተማይቱን በሙሉ ዘረፉ። 28 የበግና የፍየል መንጎቻቸውን፣ ከብቶቻቸውንና አህዮቻቸውን እንዲሁም በከተማይቱና በአካባቢው የሚገኘውን ንብረታቸውን ሁሉ ወሰዱባቸው፤ 29 ሀብታቸውን ሁሉ ዘርፈው ሴቶቻቸውንና ሕፃናቶቻቸውን ሁሉ ማርከው በየቤቱ ያገኙትን ሁሉ ይዘው ሄዱ። 30 ያዕቆብ ስምዖንና ሌዊን እንዲህ አላቸው፤ “በእኔ ላይ ከባድ ችግር አመጣችሁብኝ፤ እነሆ፣ በዚህ ድርጊት የተነሣ በዚህች ምድር የሚኖሩ ከነዓናውያንና ፌርዛውያን ይጠሉኛል፤ እኛ በቁጥር አነስተኞች ነን፣ እነርሱ ተባብረው ቢያጠቁን እኔና ቤተሰቤ እንጠፋለን።” 31 ስምዖንና ሌዊ ግን፣ “ታዲያ ሴኬም እኅታችንን እንደዝሙት አዳሪ ይድፈራትን?” አሉት።



Genesis 34:1

አሁንም

በዚህ ይህ ቃል የታሪኩን አድስ ክፍል ለማመልከት ተጠቅሞአል፡፡

ዲና

የልያ ሴት ልጅ ነች በዘፍጥረት 3ዐ:21 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ኤዊያዊ

ይህ የብሔር ስም ነው:: በዘፍጥረት 1ዐ፡17 ኤዊያዊያን የሚለውን ቃል እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የአገሩ ገዢ

ይህ ሴኬምን ሳይሆን ኤምርን ያመለክታል በዚህ ቦታ ገዢ የንጉሥ ልጅ ማለት አይደለም ይህም ኤሞር በዚያ ለሚኖሩ ሰዎች መሪ እንደነበር ነው

አስነወራት ከእርስዋም ጋር ተኛ

ሴኬም ዲናን ደፈራት (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ ቃል ወይም በተዘዋዋሪ አንድን ነገር የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ወደ ዲና ተሳበ

“በዲና ተማረከ” ዲናን እንደወደዳትና ከእርስዋ ጋር ለመሆን አንድ ነገር ወደ ዲና እንዲመጣ እንዳስገደደው ስለ ሴኬም ይናገራል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ከዲና ጋር ለመሆን እጅግ በጣም ፈልጐአል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ወይም ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በጣፈጠ አንደበት አናገራት

እንደሚወዳትና እንዲትወደው ለማድረግ ሊያሳምናት በሚስብ መንገድ አናገራት ማለት ነው

Genesis 34:4

አሁንም ያዕቆብ

“አሁን” የተጠቀመው ከታሪኩ ወደ ያዕቆብ ዳራ መረጃ ለውጥ ማድረግን ለማመልከት ነው

ያዕቆብም … እርሱ … ሰማ

“እርሱ” የሚለው ቃል ሴኬምን ያመለክታል

አስነወራት

ሰኬም በጉልበት ከእርስዋ ጋር በመተኛት ዲናን እጅግ በጣም አዋረዳት ክብርዋን ነፈጋት ማለት ነው

ታግሶ ቆዬ

ያዕቆብ ስለ ጉዳዩ ምንም አላደረገም ወይም አልተናገረም ማለት ነው:: (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 34:6

ኤሞር ያዕቆብን ሊያነጋግረው ወጣ

ኤሞር ያዕቆብን ሊያነግረው ሄደ

የያዕቆብ ወንዶች ልጆች አዘኑ

ወንዶች ልጆች እጅግም ተቆጡ ወይም ደነገጡ

እስራኤልን አስነወረ

እዚህ እስራኤል የሚለው ቃል እያንዳንዱን የእስራኤል ቤተሰብ አባል ያመለክታል እስራኤል እንደብሔር ተደፍሮአል:: አት: “የእስራኤልን ቤት አዋርዶአል” ወይም “የእስራኤልን ስዎች አሳፍሮአል” (ክፍልን እንደሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘጥቤ ይመልከቱ)

የያዕቆብን ሴት ልጅ ስለደፈረ

የያዕቆብን ልጅ ስለደፈራት

ይህ ዓይነት ተግባር መደረግ አይገባውም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “እንደዚህ አስነዋሪ ነገር ማድረግ አይገባውም ነበር” (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 34:8

ኤሞርም እንዲህ ብሎ ነገራቸው

ኤሞር ለያዕቆብና ለልጆቹ እንዲህ ብሎ ነገራቸው

በልጃችሁ ፍቅር ተነድፎአል

ፍቅር የሚለው ቃል በአንድ ወንድና ሴት መካከል የሚሆን ስሜታዊ ፍቅር ነው አት ወድዶአታልና ሊያገባት ይፈልጋል

ሚስት እንዲትሆነው እርሷን ስጡት

በአንዳንድ ባህሎች ልጆች ማግባት ያለባቸውን ወላጆች ይወስናሉ

በጋብቻ እንተሳሰር

በጋብቻ መተሣሠር ከሌላ ዘር ብሔር ባህልና ጐሣ ሰዎች ጋር መጋባት ማለት ነው:: አት: “በአናንተና በእኛ ሰዎች መጋባትን እንፍቀድ”

ምድሪቱ በእናንተ ፊት ናት

ምድሪቱ የእናንም ናት

Genesis 34:11

ሴኬም ደግሞ አባትዋን እንዲህ አለ

ሴኬም የዲናን አባት ያዕቆብን እንዲህ አለ

በእናንት ፊት ሞገስ ላግኝ እንጂ የጠየቅሁትን ሁሉ እሰጣለሁ

“ሞገስ ማግኘት” የሚለው ሀረግ በአንድ ሰው ተቀባይነትን ማረጋገጥ የሚናገር ዘይቤያዊ አነጋገር ነው ደግሞም ዓይኖች ማየትን ሲወክሉ ማየት ሀሳብን ወይም ፍረጃን ያመለክታሉ:: አት: “እንደተቀበላችሁን ካረጋገጥሁ የሚትጠይቁኝን ሁሉ እሰጣለሁ”:: (ፈሊጣዊና ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ጥሎሽ

በአንዳንድ ባህሎች በጋብቻ ጊዜ ለሙሽሪቱ ቤተሰብ ሙሽራው በገንዘብ በንብረት በእንስሳትና በሌላም መልክ ስጦታ መስጠት የተለመደ ነው

የያዕቆብ ወንዶች ልጆችም ለሴኬምና ለኤሞር የሚያታልል መልስ ሰጡ

ማታለል የሚለው ረቂቅ ስም መዋሽት እንደሚለው ግሥ ሊገለጽ ይችላል:: ነገር ግን የያዕቆብ ወንዶች ልጆች ለሴኬምና ለኤሞር በመለሱአቸው ጊዜ ዋሹአቸው (ረቂቅ ስሞችን ይመልከቱ)

ሴኬም ዲናን አስነውሮአታል

ከእርሱ ጋር እንዲትተኛ በመድፈሩ ሴኬም ዲናን እጅግ በጣም አዋርዶአታል አስነውሮአታል ማለት ነው:: በዘፍጥረት 34:5 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Genesis 34:14

እነርሱም እንዲህ አሉአቸው

የያዕቆብ ወንድ ልጆች ለሴኬምና ለኤሞር እንዲህ አሉ

እኀታችንን ብንሰጥ እንዲህ ያለውን ነገር አናደርገውም

ዲናን በጋብቻ ሊንሰጥ አንስማማም

ይህም ለእኛ ውርዴት ነው

ይህም እኛን ያሳፍረናል:: እዚህ “እኛ” የያዕቆብን ወንዶች ልጆችንና የእስራኤልን ልጆች በአጠቃላይ ያመለክታል (የሚያካትትና የማያካትት እኛን ይመልከቱ)

ሴቶች ልጆቻችንን እንሰጣችኋለን የእናንተን ሴቶች ልጆች እንወስዳለን

ይህም ከያዕቆብ ቤተሰብ የሆነ ሰው በኤሞር ምድር የሚኖረውን ሰው ያገባል ማለት ነው

Genesis 34:18

ያቀረቡትም ሃሳብ ለኤሞርና ለልጁ ለሴኬም መልካም መስሎ ታየቸው

ኤሞርና ልጁ ሴኬም የያዕቆብ ወንዶች ልጆች ባቀረቡት ሃሳብ ተስማሙ

ያሉትን ለማድረግ

ለመገረዝ

የያዕቆብ ሴት ልጅ

የያዕቆብ ሴት ልጅ ዲና

ከአባቱ ቤተሰብ ሁሉ እጅግ የተከበረው

ይህ እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: እጅግ ስለሚያከብሩት ሌሎች ሰዎች ለመገረዝ እንደሚስማሙ ሴኬም እንደተረዳ ግልጽ ማድረግ ይቻላል:: አት: “እርሱ በእነርሱ ዘንድ የተከበረ በመሆኑ የአባቱ ቤተሰብ ወንዶች ሰዎች ሁሉ ለመገረዝ እንደሚስማሙ ሴኬም ያውቅ ነበር” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)::

Genesis 34:20

ወደ ከተማቸው በር

ሕጋዊ ውሳኔ ለመወሰን በከተሞች በር መሰባሰብ በመሪዎች የተለመደ ነው

እነዚህ ሰዎች

ያዕቆብ ወንዶች ልጆቹና የእስራኤል ሰዎች

በእኛ ዘንድ የሰላም ሰዎች

እዚህ “እኛ” ኤሞር ልጁንና የተናገሩአቸው በከተማው በር ያሉ ሰዎችን ሁሉ ያቀፈ ነው (ሁሉን ያቀፈ “እኛ” ይመልከቱ)

በምድራችን ይኑሩ ይነግዱበትም

በምድሪቱ ይኑሩ ይነግዱበትም

እነሆ ምድሪቱ በእርግጥ ሰፊ ናት

ለዐረፍተ ነገሩ ትኩረት ለመስጠት ሴኬም “በእርግጥ” የሚለውን ቃል ይጠቀማል:: “እነሆ ምድሪቱ በእርግጥ ለእነርሱም ሰፊ ናት” ወይም “እነሆ ለእነርሱ የሚበቃ በቂ መሬት አለ”

ሴት ልጆቻቸውን እንውሰድ ለእነርሱም ሴት ልጆቻችንን እንስጥ

ይህ በአንዱ ቡድን ሴቶች በሌላው ቡድን ወንዶች መካከል የሚፈጸሙ ጋብቻዎችን ያመለክታል፡፡ በዘፍጥረት 34፡9 ተመሣሣይ ሀረጐችን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

Genesis 34:22

አጠቃላይ መረጃ

ኤሞርና ልጁ ሴኬም ለከተማዋ ሽማግሌዎች መናገራቸውን ቀጠሉ

አንድ ሕዝብ ሆነን ከእኛ ጋር ይቀመጡ ዘንድ በዚህ ነገር ብቻ እሺ ይሉናል እነርሱ እንደተገረዙ ወንዶቻችንን ሁሉ ብንገርዝ

ሰዎቹ ከእኛ ጋር እንደ አንድ ሕዝብ ሆነው አብረውን ለመኖር ፈቃደኞች የሚሆኑት የእኛ ወንዶች እንደ እነርሱ የተገረዙ እንደሆነ ብቻ ነው

ታዲያ እንዲህ ብናደርግ ከብቶቻቸው ንብረታቸው እንስሶቻቸው ሁሉ የእኛው ይሆኑ የለምን?

የያዕቆብ እንስሶችና ንብረቶች ለሴኬም ሰዎች እንደሚሆን ሴኬም ጥያቄ ምልክት በመጠቀም አበክሮ ይናገራል:: ይህ እንደዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: አት: “የእነርሱ እንስሳትና ንብረት ሁሉ ለእኛ ይሆናል” አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ::

Genesis 34:24

ወንዶች ሁሉ ተገረዙ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት ስለዚህ ኤሞርና ሴኬም ወንዶችን ሁሉ የሚገርዙ ነበሩአቸው (ተሻጋሪና የማይሻገር ግሥ የያዘበት ዐረፍት ነገር ይመልከቱ)

በሶስተኛውም ቀን

ሶስት ተራ ቁጥር ሶስት ነው:: ያለ ተራ ቁጥር ሊነገር ይችላል:: አት: “ከሁለት ቀን በኋላ”

ሁሉም ቆስለው ሳሉ

የከተማው ወንዶች ቆስለው ሳሉ

እያንዳንዱ ሰይፉን መዝዞ

ሰይፋቸውን መዘው

ከተማዋን ወጉት

ከተማ ሰዎችን ይወክላል አት እነርሱ የከተማይቱን ሰዎች ተዋጉ (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ጥበቃ፤ እናም ወንዶችን ሁሉ ገደሉ

ይህ እንደአዲስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ጥበቃ፡ ስምዖንና ሌዊ የከተማይቱን ወንዶች ሁሉ ገደሉ፡፡”

Genesis 34:27

ሬሳዎች

የኤሞር የሴኬምና ወንዶች ስዎቻቸው ሬሳ

ከተማዋን ዘረፉ

በከተማይቱ ያለውን ጠቃሚ ነገር ሁሉ ወሰዱ

ሰዎች እህታቸውን ስላረከሱአት

ሴኬም ብቻውን ዲናን አርክሶአት ነበር ነገር ግን የያዕቆብ ልጆች የሴኬም መላው ቤተሰብና በከተማው ያለው ሁሉ ሰው ለዚህ ድርጊት ተጠያቂ አድርገው ቆጥረዋል

አረከሳት

ከእርሱ ጋር እንዲትተኛ በመድፈር ሴኬም ዲናን አዋረዳት ወይም ክብርዋን ነፈጋት/አሳፈራት ማለት ነው:: በዘፍጥረት 34: 5 አረከሳት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

መንጎቻቸውን ወሰዱ

የያዕቆብ ልጆች የሰዎችን መንጋ ወሰዱ

ሀብቶቻቸውን ሁሉ

ንብረታቸውንና ገንዘባቸውን ሁሉ ሕጻናቶቻቸውንና ሴቶቻቸውን ሁሉ ማረኩ

Genesis 34:30

አስጨነቃችሁኝ

ለአንድ ሰው የጭንቀት ምክንያት መሆን ጭንቀት በአንድ ሰው ላይ እንደሚመጣና እንደሚቀመጥ ዕቃ ተደርጐ ተገልጾአል አት: “ትልቅ ችግሮችን ፈጥራችሁብኛል” (ዜይቤያዊ አነጋገር ይጠቀሙ)

በዚህ አገር በሚኖሩ ዘንድ እንደጥንብ አስቆጠራችሁኝ

ያዕቆብ በዙሪያው በሚኖሩ ሰዎች ዘንድ እንዲጠላ ማድረግ የያዕቆብ ልጆች እርሱን እንደ መጥፎ ሽታ እንዳደረጉ ተገልጾአል ይህ እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: አት: “በምድሪቱ በሚኖሩ ዘንድ የተጠላሁ እንዲሆን አድርጋችሁኛል” (ዜይቤያዊ አነጋገር ይጠቀሙ)

እኔ በቁጥር አነስተኞች ነኝ ቢያጠቁኝ እኔንና ቤተሰቤን ያጠፋሉ

እዚህ “እኔ” እና “እኔን” የሚሉ ቃላት ያዕቆብን ቤተሰብ በአጠቃላይ ይወክላሉ:: ያዕቆብ የቤተሰቡ መሪ ከመሆኑ የተነሳ “እኔ” ወይም “እኔን” ይጠቀማል:: አት: “ቤተሰብ አነስተኛ ነው … ተባብረው ቢነሡብኝና ቢያጠቁኝ ሁላችንንም ያጠፋሉ::” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ተባብረ ይነሡና ያጠቁኛል

ሠራዊት ይፈጥሩና ያጠቁኛል ወይም ሠራዊት ይፈጥሩና ያጠቁናል

እኔም እጠፋለሁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ያጠፉኛል ወይም ያጠፉናል ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ”

ሴኬም በሴተኛ አዳሪ/በጋለሞታ እንደሚደረግ በእኀታችን ያደርግባትን?

ሴኬም ያደረገው ጥፋትና ሞት እንደሚገባው አበክረው ለመግለጽ ሌዊና ስምዖን ጥያቄ ይጠቀማሉ:: አት: “ሴኬም እህታችንን እንደ ሴተኛ አዳሪ/ጋለሞታ አድርጐ ባልቆጠረ ነበር!” (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)


Chapter 35

1 እግዚአብሔር ያዕቆብን፣ “ተነሣና ወደ ቤቴል ሂድ፣ እዚያም ኑር። ከወንድምህ ከዔሳው ሸሽተህ በሄድህ ጊዜ ለተገለጠልህ አምላክ በዚያ መሠዊያ ሥራ አለው። 2 ስለዚህም ያዕቆብ ለቤቱ ሰዎችና አብረውት ለነበሩት ሁሉ እንዲህ አላቸው፤ “በእናንተ ዘንድ ያሉትን ባዕዳን አማልክት አስወግዱ፤ ሰውነታችሁን አንጹ፤ ልብሳችሁንም ለውጡ። 3 ተነሥተን ወደ ቤቴል እንሂድ፤ እዚያም በመከራዬ ጊዜ ለሰማኝ በሄድሁበትም ስፍራ ሁሉ ላልተለየኝ አምላክ መሠዊያ እሠራለሁ። 4 ስለዚህ በእነርሱ ዘንድ የነበሩትን ባዕዳን አማልክት ሰብስበው፣ የጆሮ ጉትቾቻቸውን አውልቀው ለያዕቆብ ሰጡት። ያዕቆብም ወስዶ ሴኬም አጠገብ ካለው ዋርካ ዛፍ ሥር ቀበራቸው። 5 ያንንም ቦታ ለቀው ሄዱ፤ እግዚአብሔርም በዙሪያቸው በነበሩት ከተሞች ሁሉ ላይ ፍርሃትና ድንጋጤ ስለለቀቀባቸው ያሳደዳቸው አልነበረም። 6 ያዕቆብና አብረውት የነበሩት ሰዎች ሁሉ በከነዓን ወደምትገኘው፣ ቤቴል ወደተባለችው ወደ ሎዛ ደረሱ። 7 ያዕቆብም በዚያ ስፍራ መሠዊያ ሠርቶ፣ ስሙን ኤል ቤቴል አለው፤ ምክንያቱም ከወንድሙ ሸሽቶ በሄደ ጊዜ እግዚአብሔር የተገለጠለት በዚህ ቦታ ነበር። 8 በዚህ ጊዜ የርብቃ ሞግዚት ዲቦራ ሞተች፣ ከቤቴል ዝቅ ብሎ በሚገኘው የዋርካ ዛፍ ሥር ተቀበረች። ከዚህ የተነሣም ያ ቦታ አሉንባኩት ተባለ። 9 ያዕቆብ ከመስጴጦምያ በተመለሰ ጊዜ እግዚአብሔር ዳግመኛ ተገለጠለትና ባረከው። 10 እግዚአብሔርም፣ “እስካሁን ስምህ ያዕቆብ ነበር፤ ከእንግዲህ ያዕቆብ ተብለህ አትጠራም፤ ነገር ግን ስምህ እስራኤል ይባላል” አለው። ስለዚህም እስራኤል ብሎ ጠራው። 11 ደግሞም እግዚአብሔር ያዕቆብን እንዲህ አለው፤ “እኔ ሁሉም ማድረግ የሚችል አምላክ ነኝ፤ ብዙ ልጆች ይኑሩህ፤ ዘርህም ይብዛ፤ የብዙ ሕዝብ አባት ሁን፤ ነገሥታትም ከአንተ ይወለዱ። 12 ለአብርሃምና ለይስሐቅ የሰጠኋትን ምድር ለአንተ እሰጣለሁ፤ ከአንተም በኋላ ይህችን ምድር ለዘርህ አሰጣለሁ።” 13 እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከተነጋገረ በኋላ ከዚያ ስፍራ ወደ ላይ ወጣ። 14 ያዕቆብ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር በተነጋገረበት ስፍራ የድንጋይ ሐውልት አቆመ፣ በሐውልቱ ላይ የመጠጥ ቁርባን አፈሰሰ፤ ዘይትም አፈሰሰበት። 15 ያዕቆብም እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር የተነጋገረበትን ስፍራ ቤቴል ብሎ ጠራው። 16 ከዚያም ከቤቴል ተነሥተው ሄዱ፤ ኤፍራታ ለመድረስ ጥቂት ሲቀራቸው ራሔልን ምጥ ያዛት፣ ምጡም ጠናባት። 17 ምጧ እየበረታ በሄደ ጊዜ አዋላጅቱ፣ “አይዞሽ አትፍሪ፤ ሌላ ወንድ ልጅ ልትወልጂ ነው” አለቻት። 18 እርስዋ ግን ልትሞት ታጣጥር ስለነበር ከመሞቷ በፊት ልጅዋን ‘ቤንኦኒ’ አለችው፤ አባቱ ግን ‘ብንያም’ አለው። 19 ራሔል ሞተች፤ ወደ ኤፍራታ በሚወስደው መንገድ በቤተልሔም ተቀበረች። 20 ያዕቆብም በራሔል መቃብር ላይ ሐውልት አቆመ፤ እስከዛሬም የራሔል መቃብር ምልክት ይኸው ሐውልት ነው። 21 ያዕቆብ ጉዞውን ቀጥሎ በዔዴር ግንብ ባሻገር ድንኳን ተክሎ ሰፈረ። 22 ያዕቆብ በዚያ ምድር ሲኖር ሳለ፣ ሮቤል ከአባቱ ቁባት ከባላ ጋር የግብረሥጋ ግንኙነት አደረገ፤ ያዕቆብም ይህን ነገር ሰማ ያዕቆብ ዐሥራ ሁለት ወንዶች ልጆች ነበሩት፣ እነርሱም፦ 23 የልያ ልጆች፦ የያዕቆብ የበኩር ልጅ ሮቤል፣ ስምዖን፣ ሌዊ፣ ይሁዳ፣ ይሳኮር፣ ዛብሎን፤ 24 የራሔል ልጆች፦ ዮሴፍ፣ ብንያም፤ 25 የራሔል አገልጋይ የባላ ልጆች፦ ዳን፣ ንፍታሌም፤ 26 የልያ አገልጋይ የዘለፋ ልጆች፦ ጋድ፣ አሴር፣ ናቸው። እነዚህ ወንዶች ልጆች ያዕቆብ በመስጴጦምያ ሳለ የተወለዱለት ናቸው። 27 ያዕቆብ በቂርያት አርባቅ (በኬብሮን) አጠገብ መምሬ በምትባል ስፍራ ወደሚኖረው አባቱ ወደ ይስሐቅ ሄደ፤ ይህም ስፍራ አብርሃምና ይስሐቅ የኖሩበት ነው። 28 ይስሐቅ መቶ ሰማንያ ዓመት ኖረ፤ 29 አርጅቶ ዕድሜ ጠግቦ ሞተ፤ ወደ ወገኖቹ ተሰበሰበ፤ ልጆቹም ዔሳውና ያዕቆብ ቀበሩት።



Genesis 35:1

ወደ ቤተል ውጣ

ውጣ የሚለው ቃል የተጠቀመው ቤቴል ከሴኬም በከፍታ ላይ ስለሚገኝ ነው

በዚያ መሠዊያ ሥራ

እግዚአብሔር ስለራሱ በሶስተኛ ሰው መንገድ ይናገራል:: አት: “ለእኔ ለአምላክህ መሠዊያ ሥራ” (እንደ አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው መግለጽን ይመልከቱ)

ለቤቱ ሰዎች እንዲህ አላቸው

ለቤተሰቡ እንዲህ አላቸው

በእናንተ ዘንድ ያሉትን ባዕዳን አማልእክት አስወግዱ

“ጣዖታትን አስወግዱ” ወይም “ሐሰተኞች አማልእክትን አስወግዱ”

ራሳችሁን አንጹ ልብሳችሁን ለውጡ

ይህ እግዚአብሔርን ለማምለክ ከመቅረብ በፊት በአካላዊና ሥነምግባራዊ ሕይወት ራስን የማንጻት ልምድ ነበር

ልብሳችሁን ለውጡ

አድስ ልብሶችን መልበስ ወደ እግዚአብሔር ከመቀረባቸው በፊት ራሳቸውን ንጹህ የማድረጋቸው ምልክት ነበር (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

በመከራዬ ቀን

በመከራዬ ጊዜ ወይም በጭንቀተ ጊዜ

Genesis 35:4

ስለዚህ ሰጡት

“ሁሉም የያዕቆብ ቤት ሰጠ” ወይም “የያዕቆብ ቤተሰብና አገልጋዮቻቸው ሰጡት”

በእጃቸው ያሉትን

እዚህ “በእጃቸው ያሉት” የእነርሱ የሆኑትን ይወክላል:: አት: “ሀብታቸው የሆኑትን ወይም ያላቸውን” (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

የጆሮ ጉትቾቻቸውን

ጉትቾቻቸውን ተገቢ ትርጉሞች እነሆ 1 የጆሮቻቸውን ወርቅ ብዙ ጣዖታትን ሊሠሩ ሊጠቀሙ ይችላሉ 2 እነዚህ ጉትቾች የሴኬም ከተማ ሰዎችን በተዋጉና ሁሉን ሰዎች በገደሉ ጊዜ የበዘበዙአቸው ናቸው:: ጉትቾች ስለኃጢአታቸው የሚያውሱ ይሆናሉና::

በዙሪያው ባሉ ከተሞች ሁሉ እግዚአብሔር ድንጋጤ ለቀቀባቸው

ያዕቆብንና ቤተሰቡን የከተሞች ሰዎች እንዲደነግጡ እግዚአብሔር ያደረገው ድንጋጤ እንደ አንድ ነገር በከተሞች እንደወደቀ ተደርጐ ተገልጾአል:: “ድንጋጤ” የተባለው ረቂቅ ስም እንደ “ፍርሃት” ሊገለጽ ይችላል:: አት: “እግዚአብሔር በዙሪያው ያሉ የከተሞች ሰዎች ያዕቆብንና በቤተሰቡን እንዲፈሩ አደረገ” ዘይቤያዊ አነጋገርና ረቂቅ ስሞችን ይመልከቱ

በከተሞች ላይ

“ከተሞች” በከተሞች የሚኖሩ ሰዎችን ይወክላሉ::

የያዕቆብ ወንዶች ልጆች

ከያዕቆብ ቤተሰብ ማንም እንዳልተጠቃ ይገልጻል ነገር ግን የያዕቆብ ሴት ልጅ ከተደፈረች በኋላ ስምዖንና ሌዊ የሴኬምን ከነዓናዊያን ዘመዶችን አጠቁአቸው በዘፍረት 34:3ዐ ያዕቆብ ሊበቀሉ ይፈልጉ ይሆናል ብሎ ፈርቶአል አት የያዕቆብ ቤት ወይም የያዕቆብ ቤተሰብ (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 35:6

ሎዛ

ይህ የከተማ ስም ነው:: በዘፍጥረት 28 19 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ኤል ቤቴል

ተርጓሚዎች የሚከተለውን የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ፡፡ “ኤል ቤተል የሚለው ስም የቤተል አምላክ ማለት ነው” (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

እግዚአብሔር የተገለጠለት በዚህ ቦታ ነበር

እግዚአብሔር ራሱን ለያዕቆብ ያስታወቀበት በዚህ ቦታ ነበር

ዲቦራ

ይህ የአንዲት ሴት ስም ነው ስምችን ስለመተርጐም ይመልከቱ

የርብቃ ሞግዚት

ሞግዚት የሌላ ሴት ልጅን የሚትንከባከብ ሴት ማለት ነው ሞግዚት እጅግ የተከበረችና በቤተሰብ ዘንድ ተቀባይነት ያላት ነች

ከቤተል ዝቅ ብሎ …. ተቀበረች

“ዝቅ ብሎ” የሚለው ሀረግ የተጠቀመው እርስዋ የተቀበረችው ቦታ ከፍታ ከቤተል ዝቅ ብሎ ስለሚገኝ ነው::

አሎንባኩት

ተርጓሚዎች የሚከተለውን የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ፡፡ “አሎንባኩት የሚለው ስም ለቅሶ ያለበት ዋርካ ዛፍ ማለት ነው” (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 35:9

ያዕቆብ ከጳዳን አራም በተመለሰ ጊዜ

በቤተል እንደነበሩ ግልጽ ማድረግ ይቻላል አት ያዕቆብም ከጳዳን አራም ከተመለሰ በኋላ በቤተል በነበረበት ጊዜ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ባረከውም

በረከት ለአንድ ሰው መልካም ነገር እንዲደረግለትና በዚያው ሰው ላይ የረከት ቃል መናገር ነው

ከእንግዲህ ያዕቆብ ተብለህ አትጠራም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ስምህ ያዕቆብ አይባልም” (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 35:11

እግዚአብሔር እርሱን እንዲህ አለው

እግዚአብሔር ያዕቆብን እንዲህ አለው

ብዛ ተባዛ

ብዙ ልጆች እንዲኖሩት ያዕቆብ ብዙ ልጆችን እንዲወልድ እግዚአብሔር ተናገረው ብዛ የሚለው እንዴት መባዛት እዳለበት ይገልጻል በዘፍጥረት 1:22 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ድርብ ቃላትና ፈሊጣዊ ንግግር ይመልከቱ)

ሕዝብና የሕዝቦች ማኀበር ከአንተ ይወጣሉ

እዚህ ሕዝብ እና ሕዝቦች የያዕቆብ ዘሮች እነዚህን ሕዝቦች እንደሚመሠርቱ ነው:: (ተመሣሣይ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ከእርሱ…. ወደ ላይ ወጣ

ወደ ላይ ወጣ የተጠቀመው ከምድር ከፍ ብሎ እግዚአብሔር እንደምኖር ለመግለጽ ነው:: አት: “እግዚአብሔር ተለየው”

Genesis 35:14

ሐውልት

ይህ በጫፉ መከሎ/ቅርጽ ያለው ትልቅ ድንጋይ ለመታሰቢያነት የቆመ ሐውልት ነው

የመጠጥ መስዋዕትንም በእርሱ ላይ አፈሰሰ ዘይትንም አፈሰሰበት

ይህም ሐውልቱን ለእግዚአብሔር የመሰደስ ምልክት ነው (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

በቴል

ተርጓሚዎች የሚከተለውን የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ፡፡ “በቴል የሚለው ስም የእግዚአብሔር ቤት ማለት ነው” (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 35:16

ኤፍራታ

ይህ የቤተልሔም ከተማ ሌላው ስም ነው

በከባድ ምጥ ውስጥ ሳለች

ምጡ አስጨንቆአት ሳለ

አዋላጅ

አንድ ሴት ልጅን በሚትወልድበት ጊዜ የሚታግዝ ሴት

ስትሞት ነፍስዋ በሚትወጣበት ጊዜ

“ነፍስ መውጣት” አንድ ሰው በሚሞትበት ጊዜ የመጨረሻ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡ አት “ከመሞትዋ በፊት በመጨረሻዋ እስትንፋስ ጊዜ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ቤንኦኒ

ተርጓሚዎች የሚከተለውን የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ፡፡ “ቤንኦኒ የምለው ስም የጭንቀቴ ልጅ ማለት ነው” (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ብንያምን

ተርጓሚዎች የሚከተለውን የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ፡፡ “ብንያምን የምለው ስም የቀኝ እጄ ልጅ ማለት ነው” የቀኝ እጅ የሚለው ሀረግ ልዩ የሚወደድ ቦታ ማለት ነው::

ተቀበረች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት “እነርሱ ቀበሩአት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በሚወስድ መንገድ

በሚወስደው መንገድ

እስከዛሬም የራሔል መቃብር ምልክት ይሄው ሐውልት ነው

ይህ እስከዛሬም የራሔል መቃብር ምልክት ነው

እስከዛሬ

እስካሁን ጊዜ ይህ ጸሐፊው፤ ይህ መልእክት የጻፈበትን ጊዜ ያመለክታል፡፡

Genesis 35:21

እስራኤልም ጉዞውን በመቀጠል

የእስራኤል ቤተሰብና አገልጋዮቹ ከእርሱ ጋር እንደነበሩ ይገልጻል የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ባላ

የራሔል ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29:29 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ::

ያዕቆብ አሥራ ሁለት ወንዶች ልጆች ነበሩት

ይህ ዐረፍተ ነገር በሚከተሉት ቁጥሮች የሚቀጥለውን አድስ አንቀጽ ይጀምራል

አሥራ ሁለት ወንዶች ልጆች

12 ወንዶች ልጆች

Genesis 35:23

ባላ

የራሔል ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29:29 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 35:26

ዘለፋ

የልያ ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29:24 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በጳዳን አራም የተወለዱ ነበሩ

ይህ በከነዓን ምድር በቤተልሔም አጠገብ የተወለደውን ብንያምን እንደማያካትት ይናገራል:: አብዛኛዎቹ የተወለዱት በጳዳን አራም ስለሆነ ይህንኑን ይጠቅሳል:: የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “በከነዓን ምድር ከተወለደው ከብንያምን በስተቀር በጳዳን አራም የተወለዱለት” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ያዕቆብ ወደ ይስሐቅ መጣ

መጣ የተባለው ሄዴ በሚለው ሊተካ ይችላል (ሄዴ እና መጣ ይመልከቱ)

መምሬ

የሔብሮን ከተማ ሌላ ስምዋ ነው የአብርሃም ወዳጆች በኖሩበት በመምሬ ስም ተጠርቶ ይሆናል በዘፍጥረት 13 18 ይህን እንዴት አንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቅርያትአርባቅ

ይህ የከተማ ስም ነው በዘፍጥረት 23 2 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 35:28

መቶ ሰማንያ ዓመት

18ዐ ዓመት (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ይስሐቅም ነፍሱን ሰጠ ሞተም

ይስሐቅም የመጨረሻውን እስትንፋስ ሰጠ ሞተም እንትንፋሱን ሰጠ/ነፍሱን ሰጠ ወይም ሞተ የሚሉ ሀረጐች በመሠረቱ አንድ ትርጉም አላቸው:: በዘፍጥረት 25:8 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት: “ይሥሐቅም ሞተ” (ድርብ ቃላት ይመልከቱ)

ነፍሱን ሰጠ

ይህ አንድ ሰው መሞቱን ትሁትና መንገድ የሚገልጽ ነው:: በዘፍጥረት 25:8 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ንኀብነት ለዛ ባለ ወይም በተዘዋዋሪ አንድን ነገር የመግለጽ ዘይቤያዊ አባባል ይመልከቱ)

ወደ ወገኖቹ ተከማቸ/ተሰበሰበ

ይስሐቅ ከሞተ በኋላ ከዚህ በፊት የሞቱ ወገኖች ነፍስ ወዳለበት ቦታ ነፍሱ ሄደች ማለት ነው ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል አት የሞቱትን የቤተሰብ አባላትን ተቀለቀለ ማለት ነው:: (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ተሻጋሪና የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮችን ይመልከቱ)

አርጅቶ እድሜ ጠግቦ

አረጅቶ እና እድሜ ጠግቦ የሚሉ ሀረጐች በመሠረቱ ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: አበክረው የሚናገሩት ይስሐቅ ብዙ ዓመታትን እንደኖረ ነው:: አት: “ብዙ ዓመታትን ኖሮ ከአረጀ በኋላ” (ድርብ አባባል ይመልከቱ)


Chapter 36

1 ኤዶም የተባለው የዔሳው የትውልድ ታሪክ የሚከተለው ነው፤ 2 ዔሳው ከነዓናውያን ሴቶችን አገባ፤ እነርሱም የኬጢያዊው የዔሎን ልጅ ዓዳን፣ የኤውያዊው የፅብዖን ልጅ ዓና የወለዳት አህሊባማ፣ 3 እንዲሁም የነባዮት እኅት የሆነችውን የእስማኤል ልጅ ቤስሞት ነበሩ። 4 ዓዳ ለዔሳው ኤልፋዝን ወለደችለት። 5 እንደዚሁም አህሊባማ የዑስን፣ የዕላምንና ቆሬን ወለደችለት፤ እነዚህ ዔሳው በከነዓን አገር የወለዳቸው ልጆቹ ናቸው። 6 ዔሳው ሚስቶቹንና ወንዶችና ሴቶች ልጆቹን፣ ቤተ ሰቦቹን በሙሉ እንደዚሁም የቀንድ ከብቶቹንና ሌሎቹንም እንስሳት ሁሉ በከነዓን ምድር ያፈራውን ሀብት እንዳለ ይዞ ከወንድሙ ከያዕቆብ ራቅ ወዳለ ቦታ ሄደ። 7 ብዙ ሀብት ስለነበራቸው አብረው መኖር አልቻሉም፣ የነበሩበትም ስፍራ ከከብቶቻቸው ብዛት የተነሣ ሊበቃቸው አልቻለም። 8 ስለዚህ ዔዶም የተባለው ዔሳው መኖሪያውን በተራራማው አገር በሴይር አደረገ። 9 በተራራማው አገር በሴይር የሚኖሩ የኤዶማውያን አባት፣ የዔሳው ዝርያዎች እነዚህ ናቸው፤ 10 የዔሳው ልጆች ስም፦ የዔሳው ሚስት የዓዳ ልጅ ኤልፋዝና የዔሳው ሚስት የቤሴሞት ልጅ ራጉኤል፤ 11 የኤልፋዝ ልጆች፦ ቴማን፣ ኦማር፣ ስፎ፣ ጎቶም ቄኔዝ፤ 12 የዔሳው ልጅ ኤልፋዝ ትምናዕ የምትባል ቁባት ነበረችው፤ እርሷም አማሌቅን ወለደችለት፤ የዔሳው ሚስት የዓዳ የልጅ ልጆች እነዚህ ናቸው። 13 የራጉኤል ልጆች፦ ናሖት፣ ዛራ፣ ሣማና ሚዛህ፤ እነዚህም ደግሞ የዔሳው ሚስት የቤሴሞት የልጅ ልጆች ናቸው። 14 የፅብዖን የልጅ ልጅ፤ የዓና ልጅ የዔሳው ሚስት አህሊባማ ለዔሳው የወለደቻቸው ልጆች፦ የዑስ፣ የዕላማና ቆሬ፤ 15 ከዔሳው ዝርያዎች እነዚህ የነገድ አለቆች ነበሩ፤ የዔሳው የበኩር ልጅ የኤልፋዝ ልጆች፦ ቴማን፣ ኦማር፣ ስፎ፣ ቄኔዝ 16 ቆሬ፣ ጎቶምና አማሌቅ፤ እነዚህ በኤዶም ምድር ከኤልፋዝ የተገኙ የነገድ አለቆች፣ የዓዳ የልጅ ልጆች ነበሩ። 17 የዔሳው ልጅ የራጉኤል ልጆች፦ ናሖት፣ ዛራ፣ ሃማና፣ ሚዛህ፤ እነዚህ በኤዶም ምድር ከራጉኤል የተገኙ የነገድ አለቆች፣ የዔሳው ሚስት የቤሴሞት የልጅ ልጆች ነበሩ። 18 የዔሳው ሚስት የአሕሊባማ ልጆች፦የዑስ፣ የዕላማና ቆሬ፤ እነዚህ ከዓና ልጅ ከዔሳው ሚስት አሕሊባማ የተገኙ የነገድ አለቆች ነበሩ። 19 እነዚህም ኤዶም የተባለው የዔሳው ልጆችና የነገድ አለቆቻቸው ነበሩ። 20 በኤዶም ምድር ነዋሪዎች የነበሩት የሴይር ልጆች የነበሩ የሖራውያን አለቆች፦ ሎጣን፣ ሦባል፣ ፅብዖን፣ ዓና፣ 21 ዲሶን፣ ኤድርና ዲሳን፤ እነዚህ በኤዶም የነበረው የሴይር ልጆች፣ በሖራውያን የነገድ አለቆች ነበሩ። 22 የሎጣን ልጆች፦ ሖሪና ሔማም የሎጣንም እኅት ቲምናዕ ትባል ነበር። 23 የሦባል ልጆች፦ ዓልዋን፣ ማኔሐት፣ ዔባልና ስፎና አውናንም፤ 24 የፅብዖን ልጆች፦ አያና፣ ዓና፤ ይህ ዓና የአባቱን የፅባዖንን አህዮች ሲጠብቅ፣ የፍልውሃ ምንጮችን በምድረበዳ ያገኘ ሰው ነው። 25 የዓና ልጆች፦ዲሶንና የዓና የሴት ልጅ አህሊባማ፤ 26 የዲሶን ልጆች፦ ሔምዳን፣ ሴስባን፣ ይትራንና ክራን፤ 27 የኤድር ልጆች፦ ቢልሐን፣ ዛዕዋንና ዓቃን፤ 28 የዲሳን ልጆች፦ዑፅና አራን። 29 የሖራውያን የነገድ አለቆች እነዚህ ነበሩ፦ሎጣን፣ ሦባል፣ፅዖን፥ ዓና፣ 30 ዶሶን፣ ኤድርና ዲሳን፤ እነዚህ በሴይር ምድር እንደየነገዳቸው የሖራውያን የነገድ አለቆች ነበሩ። 31 ንጉሥ በእስራኤል ከመንገሡ በፊት፣ በኤዶም የነገሡ ነገሥታት እነዚህ ነበሩ፦ 32 የቢዖር ልጅ ባላቅ በኤዶም ነግሦ ነበር፤ የከተማውም ስም ዲንሃባ ይባል ነበር። 33 ባላቅ ሲሞት፣ በስፍራውም የባሶራው የዛራ ልጅ ኢዮባብ ነገሠ። 34 የባሶራው የዛራ ልጅ ኢዮባብ ሲሞት የቴማኒው ሑሳም ነገሠ። 35 ሑሳም ሲሞት፣ የምድያምን ሰዎች በሞዓብ ምድር ድል ያደረጋቸው የባዳድ ልጅ ሃዳድ በምትኩ ነገሠ፤ የከተማውም ስም ዓዊት ይባል ነበር። 36 ሃዳድ ሲሞት፣ የመሥሬቃው ሠምላ በምትኩ ነገሠ። 37 ሠምላ ሲሞት፣ በወንዙ አጠገብ ያለው የርሆቦቱ ሳኦል በምትኩ ነገሠ። 38 ሳኦል ሲሞት፣ የዓክቦር ልጅ በልሐናን በምትኩ ነገሠ። 39 የዓክቦር ልጅ በልሐናን ሲሞት፣ ሃዳር በምትኩ ነገሠ፤ የከተማውም ስም ፋዑ ይባል ነበር፤ የሚስቱም ስም መሄጣብዔል ሲሆን፣ እርሷም መጥሬድ የወለደቻት የሜዛሃብ ልጅ ነበረች። 40 ከዔሳው የተገኙት የነገድ አለቆች ስም፣ እንደየነገዳቸውና እንደየአገራቸው ይህ ነው፦ ቲምናዕ፣ ዓለዋ፣ የቴት፣ 41 አህሊባማ፣ ኤላ፣ ፌኖን፣ 42 ቄኔዝ፣ ቴማን፣ ሚብሳር፣ 43 መግዲኤልና ዒራም፣ እነዚህ በያዙት ምድር እንደየይዞታቸው ከኤዶም የተገኙ የነገድ አለቆች ነበሩ። ይህም ዔሳው የኤዶማውያን አባት ነበር።



Genesis 36:1

የዔሣው ትውልድ ይህ ነው እርሱም ኤዶም ነው

ኤዶም የተባለው የዔሣው ትውልድ ይህ ነው ይህ በዘፍረት 36:1-8 የተጠቀሰውን የዔሣው ትውልድን ያስታውቃል:: አት “ይህ ኤዶም የተባለው የዔሣው ትውልድ ነው” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ዓዳ አህሊባማ

እነዚህ የዔሣው ሚስቶች ስም ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዔሎን ኬጢያዊው

“ዔሎን የኬጥ ትውልድ” ወይም “ዔሎን የኬጥ ልጅ” ይህ የአንድ ሰው ስም ነው:: በዘፍጥረት 26:34 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዓና … ጽብዖን …. ነባዮት

እነዚህ የመንዶች ሰዎች ስም ናቸው

ኤዋዊ

ይህ ትልቅ ሕዝብ ቡድንን ያመለክታል፡፡ በዘፍጥረት 1ዐ:17 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ቤሴሞት

ከዔሣው ሚስቶች የአንዷ ስም ነው:: ዘፍጥረት 26:34 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ነባዮት

ከእስማኤል ወንዶች ልጆች የአንዱ ስም ነው:: ዘፍጥረት 28:9 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:4

ዓዳ … ቤሴሞት … አህሊባማ

እነዚህ የዔሣው ሚስቶች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36:2-3 እነዚህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ኤልፋዝ ራጉኤል የዑስ የዕላም ቆሬ

እነዚህ የዔሣው ወንድ ልጆት ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:6

በከነዓን ምድር ያፈራውን ሀብት

ይህ በከነዓን ምድር በሚኖርበት ጊዜ የሰበሰበውን ወይም ያፈራውን ሁሉን ነገር ያመለክታል አት በከነዓን ምድር በሚኖርበት ጊዜ ያፈራውን ሀብት (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ወዳለ ቦታ ሄደ

ወደ ሌላ ቦታ ሂዶ በዚው ኖረ ማለት ነው:: አት: “በሌላ ቦታ ለመኖር ሄደ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሀብቶቻቸው

የዔሣውና የያዕቆብ ሀብቶች

ከከብቶቻቸው ብዛት የተነሣ ሊበቃቸው አልቻለም

ያዕቆብና ዔሣው ያሉአቸውን ከብቶቻቸውን ለማሠማራት ምድሪቱ በቂ አልነበረችም:: አት “ከብቶቻቸውን ለማሠማራት አልበቃቸውም” ወይም “ለያዕቆብ ከብቶችና ለዔሣው ከብቶች በቂ አልነበረም” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የነበሩበት ሥፍራ

የነበሩበት የሚለው ቃል ወደ አንድ ቦታ የመሄድና በዚያ መኖር ያመለክታል:: አት: “የሄዱበት ሥፍራ ወይም ቦታ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 36:9

ይህ የዔሣው ትውልድ ነው

ይህ ዐረፍተ ነገር በዘፍጥረት 36: 9-43 ያለውን የዔሣው ትውልድ ዝርዝር ያስታውቃል (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በሴይር ተራራማ አገር

በሴይር ተራራ ኖረዋል ማለት ነው:: የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “በተራራማው በሴይር አገር የኖሩ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ኤልፋዝ … ራጉኤል

እነዚህ የዔሣው ወንዶች ልጆች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36:4 እነዚህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዓዳ … ቤሴሞት

እነዚህ የዔሣው ሚስቶች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36:2-3 እነዚህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቴማን … ኦማር… ስፎ… ጎቶም… ቄኔዝ

እነዚህ የኤልፋዝ መንዶች ልጆች ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ትምናዕ

የኤልፋዝ ቁባት ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:13

ራጉኤል … ጽብዖን … የዑስ … የዕላም … ቆሬ

እነዚህ የዔሣው ወንዶች ልጆች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36:4-5 እነዚህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ናሖት ዛራ ሣማ ሚዛህ

እነዚህ የራጉኤል ወንዶች ልጆች ስሞች ናቸው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዓና … ጽብዮን

የወንድ ሰዎች ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በሴሞት … አህሊባማ

እነዚህ የዔሣው ሚስቶች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36 2 3 እነዚህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:15

ኤልፋዝ

ይህ ከዔሣው ወንዶች ልጆች የአንዱ ስም ነው በዘፍጥረት 36: 4 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቴማን … ኦማር … ስፎ … ቄኔዝ … ቆሬ … ጎቶም … አማሌቅ

የኤልፋዝ ወንዶች ልጆች ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዓዳ

ከዔሣው ሚስቶች የአንዷ ስም ነው በዘፍጥረት 36: 2-3 ስምዋን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:17

ራጉኤል … የዑስ … የዕላም … ቆሬ

እነዚህ የዔሣው ወንዶች ልጆች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36:4-5 እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ናሖት ዛራ ሣማ ሚዛህ

እነዚህ የራጉኤል ወንዶች ልጆች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36:13 እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በኤዶም ምድር

ይህም በኤዶም ምድር ኖረዋል ማለት ነው:: አት: “በኤዶም ምድር የኖሩ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በሴሞት … አህሊባማ

እነዚህ የዔሣው ሚስቶች ስሞች ናቸው:: በዘፍጥረት 36 :2-3 እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዓና

ይህ የወንድ ሰው ስም ነው በዘፍጥረት 36፡2 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:20

ሴይር

ሴይር የሚለው ቃል የአንድ ወንድ ሰውና የአንድ አገር ስም ነው

ሖሪውያን

“ሖሪውያን” የሚለው ቃል የአንድ ሕዝብ ቡድን ስም ነው:: በዘፍረት 14:6 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ(ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በምድሪቱ ነዋሪዎች

ኤዶም በተባለው በሴይር የሚኖሩ

ሎጣን ሶባል ጽብዖን ዓና ዲሶን ኤጽር ዲሳን

እነዚህ የወንዶች ሰዎች ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቲምናዕ

ይህ የሴት ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:23

ሶባል… ጽብዖን

እነዚህ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው:: በዘፍረት 36:2ዐ እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዓልዋን …ማኔሐት… ዔባል… ስፎና አውናም … አያና ዓና

እነዚህ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:25

ዓና ዲሶን ኤጽር ዲሳን

እነዚህ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው:: በዘፍረት 36: 20-21 እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

አሊህባማ

ይህ የአንዲት ሴት ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ሔምዳን ኤስባን ይትራንና ክራን ቢልሐን ዛዕዋንና ዓቃን

እነዚህ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:29

ሖሪውያን

የአንድ ሕዝበ ወገን ስም ነው:: በዘፍጥረት 14:6 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ሎጣን ሶባል ጽብዖን ዓና ዲሶን ኤጽር ዲሳን

እነዚህ የወንድ ስዎች ስሞች ናቸው በዘፍረት 36:2ዐ-21 እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በሴይር ምድር

ይህም በሴይር ምድር ኖረዋል ማለት ነው:: አት “በሴይር ምድር የኖሩ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 36:31

ቢዖር ባላቅ ኢዮባብ ዛራ

እነዚህ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የከተማውም ስም

ይህ እርሱ የኖረበት ከተማ ነበር ማለት ነው:: አት: “እርሱ የኖረበት ከተማ ስም” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ዲንሃባ ባሶራ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:34

ኢዮባብ

ይህ የወንድ ሰው ስም ነው በዘፍጥረት 36 33 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ሐሳም ሃዳድ ባዳድ ሠምላ

እነዚህ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የቴማኒው ምድር ሐሳም

ይህም ሐሳም በቴማኒ ምድር ኖሮአል ማለት ነው:: አት “በቴማኒ ምድር የኖረ ሐሳም” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ዓዊት ምሥሬቃ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቴማኒው

ቴማኒ የተባለው ሰው ትውልድ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የከተማው ስም

ይህ እርሱ የኖረበት ከተማ ነበር ማለት ነው:: አት: “እርሱ የኖረበት ከተማ ስም” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የመሥሬቃው ሠምላ

ከመሥሬቃ የሆነው ሠምላ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:37

ሠምላ

ይህ የወንድ ሰው ስም ነው:: በዘፍጥረት 36:36 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በወንዙ አጠገብ ያለው የርሆቦቱ ሳኦል በምትኩ ነገሠ

ሳኦል በርሆቦት ይኖር ነበር:: ርሆቦት በኤፍራጥስ ወንዝ አጠገብ ነው:: ይህ መረጃ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “ከዚያም ሳኦል በምትኩ ነገሠ:: እርሱም ከኤፍራጥስ ወንዝ አጠገብ ከነበረችው ከርሆቦት ነው (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ርሆቦት ፋዑ

የቦታዎች ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የከተማው ስም

ይህ እርሱ የኖረበት ከተማ ነበር ማለት ነው:: አት: “እርሱ የኖረበት ከተማ ስም” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የሜዛሃብ ልጅ መጥሬድ የወለደቻት

እርሷም የሜዛሃብ ልጅ መጥሬት የወለደቻት ነበረች

መሄጣብኤል

የሴት ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 36:40

የነገድ አለቆች

የነገድ መሪዎች

እንደየስማቸው እንደየነገዳቸውና እንደየአገራቸው

ነገዳቸውና አገራቸው በአለቆቻው ወይም በመሪዎቻቸው ስም ተሰይሞአል:: አት: “የነገዶቻቸውና የሚኖሩባቸው አገራቸው በመሪዎቻቸው ስም ተሠይሞአል” የእነርሱ ስሞች እነሆ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ቲምናዕ ዓልዋ የቴት አህሊባማ ኤላ ፋኖን ቄኔዝ ቴማን ሚብሳር መግዲኤልና ዒራም

እነዚህ የህዝብ ወገኖች ወይም የነገዶች ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በግዛታቸው ወይም በሠፈሩባቸው ምድር

“በሚኖሩባቸው ቦታዎች” ወይም “በኖሩባቸው ቦታዎች”

ይህም ዔሣው ነው

ይህ የስም ዝርዝር ዔሣው ነው የተባለው ይህ የትውልዱ አጠቃላይ ዝርዝር ነው ማለት ነው:: አት: “ይህ የዔሣው ትውልድ ዝርዝር ነው” (ተዛማጅ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)


Chapter 37

1 የዕቆብ አባቱ በኖረበት በከነዓን ምድር ተቀመጠ። 2 የያዕቆብ ትውልድ ታሪክ ይህ ነው። ዮሴፍ የዐሥራ ሰባት ዓመት ወጣት በነበረ ጊዜ፣ ከአባቱ ሚስቶች ከባላቅና ከዘለፋ ከተወለዱት ወንድሞቹ ጋር የአባቱን በጎችና ፍየሎች ይጠብቅ ነበር። እርሱም ስለወንድሞቹ ድርጊት ለአባቱ መጥፎ ወሬ ይዞለት መጣ። 3 እስራኤል ዮሴፍን በስተርጅናው ስለወለደው፣ ከልጆቹ ሁሉ አብልጦ ይወደው ነበር፣ በኅብረ ቀለማት ያጌጠ እጀ ጠባብም ሰፋለት። 4 ወንድሞቹም አባታቸው ከእነርሱ አብልጦ የሚወደው መሆኑን ሲያዩ ዮሴፍን ጠሉት፤ በቅን አንደበት ሊያናግሩት አልቻሉም። 5 ዮሴፍ ሕልም አለመ፤ ሕልሙንም ለወንድሞቹ ሲነግራቸው የባሰ ጠሉት፤ 6 እርሱም እንዲህ አላቸው፤ “ያየሁትን ሕልም ልንገራችሁ አድምጡኝ” 7 ‘እኛ ሁላችን በእርሻ ውስጥ ነዶ እናስር ነበር፤ የእኔ ነዶ ተነሣና ቀጥ ብሎ ቆመ፤ የእናንተ ነዶዎች ዙሪያውን ተሰብስበው ለእኔ ነዶ ሰገዱለት’” 8 ወንድሞቹም፣ “ታዲያ በእኛ ላይ ንጉሥ ሆነህ ልትገዛን ታስባለህን?” ብለው ጠየቁት። ስለ ሕልሙና ስለተናገረው ቃል ከፊት ይልቅ ጠሉት። 9 እንደ ገናም ሌላ ሕልም አለመ፤ ለወንድሞቹም እነሆ፣ ሌላ ሕልም አለምሁ፣ ፀሐይና ጨረቃ፣ ዐሥራ አንድ ክዋክብትም ሲሰግዱልኝ ዐየሁ” ብሎ ነገራቸው። 10 ይህንኑ ለወንድሞቹ የነገራቸውን ሕልም ለአባቱም በነገረው ጊዜ፣ አባቱ፣ “ይህ ምን ዐይነት ሕልም ነው? እኔና እናትህ ወንድሞችህም በፊትህ ወደ ምድር ተጎንብሰን በርግጥ ልንሰግድልህ ነው?” ሲል ገሠጸው። 11 ወንድሞቹ ቀኑበት፤ አባቱ ግን ነገሩን በልቡ ያዘው። 12 አንድ ቀን የዮሴፍ ወንድሞች የአባታቸውን መንጋዎች ይዘው ወደ ሴኬም ተሰማሩ፤ 13 እስራኤልም ዮሴፍን፣ “እንደምታውቀው ወንድሞችህ መንጎቹን በሴኬም አካባቢ አሰማርተዋል፤ በል ተነሥ፣ ወደ እነርሱ ልላክህ” አለው። ዮሴፍም፣ “እሺ እሄዳለሁ” አለ። 14 አባቱም፣ “በል እንግዲህ ሄድና የወንድሞችህንና የመንጋዎቹን ደኅንነት አይተህ ንገረኝ” አለው። በዚህ ዓይነት እስራኤል ዮሴፍን ከኬብሮን ሸለቆ ላከው። ዮሴፍም ሴኬም በደረሰ ጊዜ፣ 15 ሜዳ ላይ ወዲያ ወዲህ ሲባዝን አንድ ሰው አግኝቶት፣ “ምን እየፈለግህ ነው?” ሲል ጠየቀው። 16 ዮሴፍም፣ “ወንድሞቼን እየፈለግኋቸው ነው፤ መንጎቻቸውን የት እንዳሰማሩ ልትነግረኝ ትችላለህ?” አለው። 17 ሰውዬውም፣ “ከዚህ ሄደዋል፤ ደግሞም ‘ወደ ዶታይን እንሂድ’ ሲሉ ሰምቻቸዋለሁ” አለው። ከዚያም ዮሴፍ ወንድሞቹን ፍለጋ ሄደ፣ በዶታይን አቅራቢያም አገኛቸው። 18 ወንድሞቹም ዮሴፍ ወደ እነርሱ ሲመጣ በሩቅ ዐዩት፣ ወደ ነበሩበትም ስፍራ ከመድረሱ በፊት ሊገድሉት ተማከሩ። 19 እነርሱ እንዲህ ተባባሉ፦ “ያ ሕልም አላሚ መጣ፤ 20 ኑ እንግደለውና ከጉድጓዶቹ በአንዱ ውስጥ እንጣለው፤ ከዚያም፣ ‘ክፉ አውሬ ነጥቆ በላው’ እንላለን፤ እስቲ ሕልሞቹ ሲፈጸሙ እናያለን።” 21 ሮቤል ግን ይህን ምክር ሲሰማ ከእጃቸው ሊያድነው ፈለገ እንዲህም አለ፤ “አንግደለው፤ 22 የሰው ደም አታፍስሱ፣ ከምትገድሉት ይልቅ በዚህ በበረሃ ባለው ጉድጓድ ውስጥ ጣሉት” አላቸው። ሮቤል ይህን ያለው ሕይወቱን ከእጃቸው አትርፎ ወደ አባቱ ሊመልሰው ዐስቦ ነበር። 23 ዮሴፍ ወደ ወንድሞቹ እንደደረሰ፣ የለበሳትን በኅብረ ቀለማት የጌጠች እጀ ጠባቡን ገፈፉት፤ 24 ይዘውም ወደ ጉድጓድ ጣሉት፤ ጉድጓዱም ውሃ የሌለበት ደረቅ ነበር። 25 ምግባቸውን ለመብላት ተቀመጡ፤ አሻግረው ሲመለከቱም ከገለዓድ የሚመጡ እስማኤላውያን ነጋዴዎች ጓዛቸውን በግመሎች ላይ ጭነው ተመለከቱ። ነጋዴዎቹ ሽቶ፣ በለሳን፣ ከርቤ በግመሎቻቸው ጭነው ወደ ግብፅ የሚወርዱ ነበሩ። 26 ይሁዳም ወንድሞቹን እንዲህ አላቸው፤ “ወንድማችንን መግደልና አሟሟቱን መደበቅ ምን ይጠቅመናል? 27 ከዚህ ይልቅ ለእስማኤላውያን ነጋዴዎች እንሽጠው፤ እጃችንን ግን በእርሱ ላይ አናንሳ። ምንም ቢሆን የሥጋ ወንድማችን ነው” ወንድሞቹም በሃሳቡ ተስማሙ። 28 የምድያም ነጋዴዎች የሆኑ እስማሴላውያን በዚያ በኩል ያልፉ ነበር፤ ስለዚህ ወንድሞቹ ዮሴፍን ከጉድጓድ ጎትተው በማውጣት ለእነዚህ እስማኤላውያን በሃያ ብር ሸጡላቸው፣ እነርሱም ወደ ግብፅ ይዘውት ሄዱ። 29 ሮቤል ወደ ጉድጓዱ ተመልሶ ሲያይ፣ ዮሴፍን በማጣቱ ልብሱን በሐዘን ቀደደ። 30 ወደ ወንድሞቹም ተመልሶ፣ “እነሆ፣ ልጁ እዚያ የለም! እንግዲህ እኔ ወዴት ብሄድ ይሻለኛል?” አለ። 31 ከዚህ በኋላ አንድ ፍየል አረዱና የዮሴፍን ልብስ በደም ነከሩት። 32 በኅብረ ቀለማት ያጌጠችውን እጀ ጠባብ ወደ አባታቸው ወስደው፣ “ይህን ወድቆ አገኘነው፤ የልጅህ እጀ ጠባብ መሆን አለመሆኑን እስቲ እየው” አሉት። 33 እርሱ የልጁ ልብስ መሆኑን ተረድቶ፣ “ይህማ የልጄ እጀ ጠባብ ነው! ፤ ክፉ አውሬ በልቶታል፣ በእርግጥም ዮሴፍ ተቦጫጭቆአል” አለ። 34 ከዚህ በኋላ ያዕቆብ ልብሱን ቀደደ፤ ማቅም ለብሶ ስለ ልጁ ብዙ ቀን አለቀሰ፤ 35 ወንዶችና ሴቶች ልጆቹም ሁሉ ሊያጽናኑት መጡ፤ እርሱ ግን ሊጽናና አልቻለም፣ “በሐዘን እንደተኮራመትሁ ልጄ ወዳለበት መቃብር እወርዳለሁ” አለ። ስለ ልጁም አለቀሰ። 36 በዚህ ጊዜ የምድያም ነጋዴዎች ዮሴፍን ወደ ግብፅ ወስደው፣ ከፈርዖን ሹማምንት አንዱ ለነበረው ለዘበኞች አለቃ፣ ለጲጥፋራ ሸጡት።



Genesis 37:1

አባቱ በቆየበት አገር በከነዓን ምድር ተቀመጠ

አባቱ በኖረበት በከነዓን ምድር ተቀመጠ

የያዕቆብ ትውልድ ታሪክ ይህ ነው

ይህ ዐረፍተ ነገር በዘፍጥረት 37: 1-5ዐ:26 ያለውን የያዕቆብን ትውልድ ያስታውቃል፡፡ እዚህ ያዕቆብ መላው በተሰቡን ይወክላል፡፡ አት “ይህ የያዕቆብ ቤተሰብ ታሪክ ነው” (ክፍልን እንደሙሉና ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

አሥራ ሰባት ዓመት ዕድሜ

17 ዓመት ዕድሜ

ባላ

ይህ የራሔል ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29: 29 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዘለፋ

ይህ የልያ ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29: 24 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ሚስቶች

እነዚህ ሴቶች ልጅ እንዲወልዱ ዘንድ ለያዕቆብ የተሰጡ የልያና የራሔል አገልጋዮች ናቸው

ስለእነርሱ መጥፎ ወሬ

ስለወንድሞቹ መጥፎ ወሬ

Genesis 37:3

አሁንም

ይህ ቃል ታሪኩ ስለ እስራኤልና ዮሴፍ ዳራ መረጃ መቀየሩን የሚያመለክት ነው (ዳራ መረጃ ይመልከቱ)

ስለወደደው

ይህ ወንድማማች ፍቅር ወይም ጓደኛ ፍቅር ወይም ቤተሰብ ፍቅር ያመለክታል ይህ በጓደኛሞችና በቤተሰብ መካከል የሚገለጽ ተፈጥሮአዊ የሰው ልጅ ፍቅር ነው

በስተርጅናው

እስራኤል በአረጀ ጊዜ ዮሴፍን ወልዶአል ማለት ነው:: አት: “እስራኤል በአረጀ ጊዜ የተወለደው” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እርሱ ለእርሱ ……አደረገለት

እስራኤል ለዮሴፍ ..አደረገለት

በኀብረቀለማት ያገጤ እጄ ጠባብ

እጅግ የሚያምር እጄ ጠባብ

በቅን አንደበት ሊያናግሩት አልቻሉም

በሰላም ሊያናግሩት ዘንድ አልቻሉም

Genesis 37:5

ዮሴፍም ሕልምን አለመ ሕልሙንም ለወንድምቹ ሲነግራቸው የባሰ ጠሉት

ይህ በዘፍጥረት 37:6-11 የተቀመጠው ታሪክ ማጠቃለያ ሀሳብ ነው::

የበለጠውኑ ጠሉት

የዮሴፍ ወንድሞች ከዚህ በፊት ከሚጠሉት በላይ ጠሉት

ያየሁትን ይህን ሕልም ልንገራችሁ አድምጡኝ

ሕልሜን ልንገራችሁ አድምጡኝ

Genesis 37:7

አጠቃላይ መረጃ

ስለሕልሙ ዮሴፍ ለወንድሞቹ ይናገራል

እነሆ

“እነሆ” የሚለው ቃል ለሚቀጥለው አስደናቂ ሃሳብ ትኩረት እንዲሰጠው ያነቃል

እኛ ሁላችን

“እኛ” የሚለው ቃል ዮሴፍና ወንድሞቹን ሁሉ ያጠቃልላል (ሁሉን ያቀፈ እኛ ይመልከቱ)

ነዶ እናሥር ነበር

እህል ከታጨደ በኋላ ፍሬው ከገለባው እስኪበጠር ድረስ በየነዶው ታሥሮና ተከምሮ ይጠበቃል

እንሆ

“እነሆ” የሚለው ቃል ዮሴፍ ባየው እንደተደነቀ ይገልጻል

የእኔ ነዶ በድንገት ተነሥታ ቀጥ ብላ ቆመች የእናንተ ነዶዎች ዙሪያዋን ከበው ለእኔ ነዶ ሰገዱላት

እዚህ እንደሰው ነዶዎች ሲቆሙና ሲሰግዱ ይታያል እነዚህ ነዶዎች ዮሴፍንና ወንድምቹን ይወክላሉ (በሰውኛ መንገድ አገላለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በላያችን ልትነግሥብን ይሆን? ልትገዛ ይሆን?

እነዚህ ሁለቱም ሀረጐች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው የዮሴፍ ወንድሞች ጥያቄዎችን በመጠቀም ዮሴፍን ማላገድ ጀመሩ እነዚህ በዐረፍተ ነገሮች መልክ ሊገለጹ ይችላሉ አት ንጉሣችን አትሆንም እኛም ለአንተ አንሠግድም (አግናኝ ጥያቄዎችንና ተዛማጅ ተመሣሣይ አባባል ይመልከቱ)

እኛን ልትገዛ

እኛ የሚለው ቃል ዮሴፍን ሳይሆን ወንድሞቹን ያመለክታል (ሁሉን አቀፍና ሁሉን የማያቅፍ “እኛ” ይመልከቱ)

ለሕልሙና ለተናገረው ቃል

ስለ ሕልሙና ልሰተናገረው ቃል

Genesis 37:9

ሌላ ሕልም አለመ

ዮሴፍ ሌላ ሕልም አለመ

አሥራ አንድ ከዋክብት

11 ከዋክብት ቁጥሮች ይመልከቱ

አባቱ ገሠጸው እንዲህም አለው

እስራኤልም ገሠጸው አለውም

ይህ ያየሄው ሕልም ምንድን ነው? እኔና እናትህ ወደ ምድር ተጐንብሰን ልንሰግድል ነው?

እስራኤል ዮሴፍን ለማረም ጥያቄዎችን ይጠቀማል:: ይህ እንደ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል:: አት: “ይህ ያየሄው ሕልም ትክክል አይደለም:: እኔ እናትህና ወንድሞችህ በፊትህ አንሰግድልህም!” (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ቀኑበት

አንድ ሰው ስኬታማና እጅግ ታዋቂ ከመሆኑ የተነሣ በቁጣ መሞላት ማለት ነው

ነገሩን በልቡ ያዘው

ስለዮሴፍ ሕልም ትርጉም ማሰቡን ቀጠለ ማለት ነው:: አት: “የሕልሙ ትርጉም ምን እንደሆን ማሰቡን ቀጠለ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 37:12

ወንድሞችህ በሰኬም በጎችን ይጠብቁ አይደለምን?

እስራኤል በንግግሩ ውስጥ ጥያቄ ይጠቀማል:: ይህ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ወንድሞችህ በሰኬም በጎችን ይጠብቃሉ” (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ለመሄድና ወንድሞቹን ለማየት ዮሴፍ እንዲዘጋጅ እስራኤል መጠየቁን የሚገልጽ ነው:: አት “ተዘጋጅ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

እነሆኝ

ለመሄድ ተዘጅቸአለሁ(ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

እርሱም እርሱን አለው

እስራኤል ዮሴፍን አለው

ወሬያቸውን አምጣልኝ

ወንድሞቹና በጎቹ እንዴት እንደሆኑ ዮሴፍ ተመልሶ እንዲነግረው እስራኤል ይፈልጋል አት ተመልሰው ያገኘሄውን ንገረኝ ወይም ርፖርት አቅርብልኝ (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በሸለቆው

ከሸለቆው

Genesis 37:15

እነሆ ዮሴፍ ሜዳ ላይ ወዲያና ወዲህ ሲባዝን ነበር አንድ ሰውም ዮሴፍን አገኘው

ዮሴፍ ወዲያና ወዲህ ሲባዝን አንድ ሰው ዮሴፍን አገኘው

እነሆ

በትልቁ ታሪክ ስለሌላ ክስተት መጀመሩን የሚያመለክት ነው በቀደሙ ክስተቶች ከነበሩ ሌሎች ሰዎች የሚያሳትፍ ነው በእርስዎ ቋንቋ ይህ የሚገለጽበት መንገድ ሊኖር ይችላል

ምን እያየህ ነው ?

ምን እየፈለግህ ነው?

ወዴት ነው እባክህ ንገረኝ

ወዴት እንደሆነ እባክህ ንገረኝ

ዶታይን

ከሰኬም 22 ኪሎ ሜትር ያህል ርቀት ያለ ቦታ ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 37:18

በሩቅ አዩት

በሩቅ እያለ የዮሴፍ ወንድሞች አዩት

ይገድሉት ዘንድ በእርሱ ላይ ተማከሩ

እርሱን ለመግደል አቀዱ

ያ ሕልም ዐላሚ መጣ

ያ ባለ ሕልም ይሄው መጣ

ስለዚህ አሁንም ኑ

ይህ አባባል ወንድሞቹ ዕቅዳቸውን መተግበር መጀመራቸውን ያሳያል:: አት: (ስለዚህ አሁን ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ክፉ አውሬ

አደገኛ አውሬ ወይም ሰው ጨካኝ አውሬ

ቦጫጭቆ በላው

ንጥቆ በላው

ከሕልሞቹም የሚሆነውን እናያለን

ወንድሞቹ ሊገድሉት አቅደዋልና ስለዚህ እስከሞተ ድረስ ሕልሞቹ ይፈጸሙ እንደሆን መናገራቸው አሽሙራዊ/ሽሙጣዊ አባባል ነው:: አት “እስቲ ሕልሞቹ ሲፈጸሙ እናያለን” (በአሽሙር/ሽሙጥ መንገድ የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 37:21

ይህን ሰማ

እነርሱ የመከሩትን ሰማ

ከእጃቸው

ከእጃቸው የሚለው አባባል ሊገድሉት ያቀዱትን የወንድሞቹን እቅድ ያመለክታል:: አት “ከእነርሱ” ወይም “ከእቅዳቸው” (ተዛማጅ ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ሕይወቱን አናጥፋ

ሕይወት ማጥፋት የሚለው ሀረግ አንድን ሰው ስለመግደል በንኀብነት ወይም ለዛ ባለ ቃል በተዘዋዋሪ የሚገልጽ ነው፡፡ አት፡ “ዮሴፍን አንግደለው” (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ ቃል በተዘዋዋራ መንገድ የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ደም አታፍስሱ

በግሡ አሉታዊነት ተጨምሮበታል ደግሞም ደምን ማፍሰስ አንድን ሰው ስለመግደል በንኀብነት ወይም ለዛ ባለ ቃል በተዘዋዋሪ የሚገልጽ ነው፡፡ አት የማንኛውንም ሰው ደም አታፍስሱ ወይም አትግደሉት (በአሉታዊነት አዎንታዊነትን የመግለጽ ዘይቤና ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ ቃል በተዘዋዋራ መንገድ የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

እጃችሁን አታንሡበት

አታቆስሉት ወይም አትጉዱት ማለት ነው አት አትጉዱት (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ከእጃቸው ሊያተርፈው

ይህ እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ሊገለጽ ይችላል:: “ሮቤል ይህ ያለው ዮሴፍን ሊታርፈው ዘንድ ነው”

ከእጃቸው

ከእጃቸው የሚለው አባባል ሊገድሉት ያቀዱትን የወንድሞቹን እቅድ ያመለክታል:: አት “ከእነርሱ” ወይም “ከእቅዳቸው” (ተዛማጅ ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ሊመልሰው

እናም ሊመልሰው

Genesis 37:23

እንደ ደረሰ

ይህ ሐረግ በታሪኩ ተፈላጊ ክስተት ለመጠቆም ተጠቅሞአል በቋንቋህ እንዲህ ዓይነት ካለ በዚህ ቦታ ሊጠቀሙ ይችላሉ

በኀብረ ቀለማት ያገጠች እጀ ጠባቡን ገፈፉት

በኀብረ ቀለማት ያገጠች እጀ ጠባቡን ከላዩ ላይ ቀደዱት

ያገጠች ልብስ

ያገጠች እጀ ጠባብ፤ በዘፍጥረት 37:3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

Genesis 37:25

እንጀራም ሊበሉ ተቀመጡ

እንጀራ በአጠቃላይ መግብን ያመለክታል አት ምግባቸውን ለመብላት ተቀመጡ ወይም የያዕቆብ ወንድሞች ምግባቸውን ሊበሉ ተቀመጡ (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግልጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ዐይኖቻቸውንም አንስተው አዩ እነሆም… የግመል ጓዝ

እዚህ አንስተው አዩ አንድሰው በውኑ አይኑን እንሰቶ እንደሚያይ ተደርጐ ተነግሮአል ደግሞም እነሆ የሚለው ቃል ሰዎች ላዩት ትኩረት ለመስጠት ተጠቅሞአል:: አት: “አይኖቻቸውን አነሡ እናም ወዲያውም የግመል ጓዝ አዩ” (ዘይቤያዊ አባባል ይመልከቱ)

ተሸክመው

ጭነው

ኬርቤ

ቅመማቅመም

በለሳን

የቆዳ ቁስለትን የሚፈውስና የሚከለክል ጣፋጭ ጣዕም ያለው ቅባታማ ነገር “መድኃኒት”

ጭነው ወደ ግብጽ የሚወርዱ

ወደ ግብጽ የሚያመጡ ይህ ግለጽ ሊደረግ ይችላል አት ለመሸጥ ወደ ግብጽ የሚወርዱ ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ

ወንድማችንን መግደልና ደሙን መሸሸግ ምን ይጠቅማናል?

ይህ እንደዐረፍተ ነገር ሊገለጽ ይችላል:: አት “ወንድማችንን በመግደልና አሟሟቱን በመደበቅ እንጠቀምም” (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ደሙን መሸሸግ

የዮሴፍን ሞት በደበቅን የሚገልጽ ምሳሌዊ አነጋገር ነው:: አት “አሟሟቱን መደበቅ” (ዘይቤያዊ አባባል ይመልከቱ)

Genesis 37:27

ለእስማኤላዊያን

የእስማኤል ዘር ለሆኑ ለእነዚህ ሰዎች

እጃችንን በእርሱ ላይ አናንሳ

ይህም “አናቆስለው” ወይም “አንጉዳው” ማለት ነው አት: “አንጉዳው” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ወንድማችን ሥጋችን ነው

ሥጋ የሚለው ዘመድ ለሚለው ቃለ የሚቆም ምትክ ቃል ነው:: አት: “እርሱ የሥጋ ዘመዳችን ነው” (ተዛማጅ ምትክ ቃላትን የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ወንድሞቹም የእርሱን ነገር ሰሙት

የይሁዳ ወንድሞች ሰሙት ወይም የይሁዳ ወንድሞች በሐሳቡ ተስማሙ

ምድያማዊያን ….. እስማኤላዊያን

ሁለቱም ስሞች የዮሴፍ ወንድሞች ያገኙአቸው ተመሣሣይ ነጋዴዎችን ያመለክታል

ለሃያ ጥሬ ብር

ለሃያ ጥሬ ብር ዋጋ (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ዮሴፍን ወደ ግብጽ የዘውት ሄዱ

ዮሴፍን ወደ ግብጽ ወሰዱት

Genesis 37:29

ሮቤል ወደ ጉድጓዱ ተመልሶ ሲያይ ዮሴፍን በማጣቱ

ሮቤል ወደ ጉድጓዱ ተመልሶ ዮሴፍን በማጣቱ እነሆ ተገረመ:: “እነሆ” የሚለው ቃል ሮቤል ዮሴፍ በሄዱን ባወቀ ጊዜ መገረሙን ያሳያል::

ልብሱን ቀደደ

ይህ የጥልቅ ጭንቀትና ሀዘን ምልክት ነው:: ይህ በግልጽ ሊገለጽ ይችላል:: አት: እጅግም ስላዘነ ልብሱን ቀደደ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ብላቴናው የለም እንግዲህ እኔ ወዴት እሄዳለሁ?

የዮሴፍ መጥፋቱን ችግር ትኩረት ለመስጠት ሮቤል ጥያቄ ይጠቀማል:: አት: “ብላቴናው ሄዶአል እንግዲህ ወደ ቤት መመለስ አልችልም” (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

Genesis 37:31

የዮሴፍ እጀ ጠባብ

አባቱ ያዘጋጀለት ያጌጠችውን እጀ ጠባብ ያመለክታል

ደም

የፍዬል ደም

አምጥተው

እጀ በባቡን አምጥተው

ቦጫጭቆ በልቶታል

በልቶታል

በእርግጥም ዮሴፍ ተቦጫጭቆአል

ያዕቆብ የዮሴፍን አካል ክፉ አውሬ እንደገነጣጠለ አሰበ:: አት: “በእርግጥም ዮሴፍን ቦጫጭቆታል” (ተሻጋሪና የማይሻገር ግሥ ይመልከቱ)

Genesis 37:34

ያዕቆብ ልብሱን ቀደደ

ይህ ጥልቅ መጨነቅንና ሀዘንን የሚያመለክት ነው ይህ በግልጽ ሊገለጽ ይችላል አት ያዕቆብ እጅግ ስላዘነ ልብሱን ቀደደ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በወገቡም ማቅ ታጥቆ

ወገብ የሰውነት መሀከለኛው አካል ነው አት ማቅ ለብሶ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ተነሡ

እዚህ አባታቸውን ለማጽናናት የልጆች መጥጣት እንደ መነሣት ተደርጐ ተገልጾአል:: አት: “ወደ እርሱ መጡ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እርሱ ግን ሊጽናና ባለመቻሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ነገር ግን እንዲያጽናኑት አልፈቀደም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ወደ ሙታን ሥፍራ እያዘንሁ እወርዳለሁ

ከዛሬ ጀምሮ እስከሚሞት ድረስ እንደሚያዝን ይገልጻል:: አት: “በሚሞትበትና ወደ ሙትን ሥፍራ በሚወርድበትም ጊዜም በእርግጥ እያዘንኩ ይሆናል” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ምድያማዊያን ሸጡት

ምድያማዊያን ዮሴፍን ሸጡት

ለዘበኞች አለቃ

ንጉሡን ለሚጠብቁ ዘበኞች መሪ


Chapter 38

1 በዚያም ወራት ይሁዳ ከወንድሞቹ ተለይቶ ሒራ ወደተባለ ዐዱላማዊ ሰው ዘንድ ሄደ፣ መኖሪያውንም 2 እዚያም ሳለ፣ ይሁዳ የከነዓናዊውን የሴዋን ሴት ልጅ ዐየ፤ እርሷንም አግብቶ የግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጸመ። 3 እርሷም አርግዛ ወንድ ልጅ ወለደችለት፤ ስሙንም ዔር ብላ ጠራችው። 4 እንደገናም አረገዘችና ወንድ ልጅ ወለደችለት፤ ስሙንም አውናን አለችው። 5 አሁንም ደግማ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ስሙንም ሴሎም ብላ ጠራችው፣ እርሱንም የወለደችው ክዚብ በተባለ ቦታ ነበር። 6 ይሁዳ የመጀመሪያ ልጁን ዔርን ትዕማር ከምትባል ልጃገረድ ጋር አጋባው። 7 የይሁዳ የበኩር ልጅ ዔር ግን በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ነበር፤ እግዚአብሔርም ቀሠፈው። 8 ይሁዳ አውናንን፣ “ዋርሳዋ እንደመሆንህ ከወንድምህ ሚስት ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት በመፈጸም የወንድምህን ስም የሚያስጠራለት ዘር ተካለት አለው። 9 አውናን ግን የሚወለደው ልጅ የእርሱን ስም የሚያስጠራ እንደማይሆን ስላወቀ፣ ከወንድሙ ሚስት ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት በፈጸመ ቁጥር የወንድሙን ስም የሚያስጠራ ልጅ እንዳይወለድ ዘሩን በምድር ላይ ያፈስ ነበር። 10 ይህም በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ሆኖ ስለተገኘ፣ እርሱንም እግዚአብሔር በሞት ቀሠፈው። 11 ከዚያም ይሁዳ ምራቱን ትዕማርን፣ “ልጄ ሴሎም ለአካለ መጠን እስኪደርስ ድረስ ወደ አባትሽ ቤት ሄደሽ መበለት ሆነሽ ብትኖሪ ይሻላል” አላት፤ ይህን ያለውም፤ ሴሎም እንደወንድሞቹ ተቀሥፎ ይሞትብኛል ብሎ ስለፈራ ነበር። ትዕማርም እንዳላት ሄደች፤ በአባቷም ቤት ተቀመጠች። 12 ከብዙ ጊዜ በኋላ የሹዓ ልጅ፣ የይሁዳ ሚስት ሞተች። ይሁዳ ከሐዘኑ ከተጽናና በኋላ ከዓዶላማዊው ከሒራ ጋር የበጎቹን ጠጉር የሚሸልቱ ሰዎች ወዳሉበት ወደተምና ሄደ። 13 ሰዎቹም ለትዕማር፣ “አማትሽ የበጎቹን ጠጉር ወደሚሸልቱ ሰዎች ዘንድ ወደተምና እየሄዱ ነው” አሏት። ይህን እንድሰማች 14 የመበለትነት ልብሷን አውልቃ፣ ማንነቷ እንዳይታወቅ ፊቷን በሻሽ ተከናንባ ወደ ተምና በሚወስደው መንገድ ዳር ባለች ኤናይም በተባለች ከተማ መግቢያ በር ላይ ተቀመጠች፤ ይህን ያደረገችው፣ ሴሎም ለአካለ መጠን ቢደርስም፣ እርሷን እንዲያገባ አባቱ አለመፈለጉን ስላወቀች ነው። 15 ፊቷ በሻሽ ተሸፋፍኖ ሲያያት፣ ይሁዳ ዝሙት አዳሪ መሰለችው። 16 ምራቱ መሆኗን ባለማወቁ፣ እርሷ ወዳለችበት ወደ መንደሩ ዳር ጠጋ ብሎ፣ “እባክሽን አብሬሽ ልተኛ” አላት። እርሷም፣ “አብሬህ ብተኛ ምን ትሰጠኛለህ?” ብላ ጠየቀችው። 17 “ከመንጋዬ መካከል አንድ የፍየል ጠቦት እልክልሻለሁ” አላት። እርሷም “ጠቦቱን እስክትልክልኝ ድረስ ምን መያዣ ትሰጠኛለህ?” ብላ ጠየቀችው። 18 “ታዲያ ምን መያዣ ልስጥሽ?” አላት። እርሷም፣ “የማኅተም ቀለበትህን ከነማሰሪያው፣ እንደዚሁም ይህን በትርህን ስጠኝ” አለችው። የጠየቀችውን ሁሉ ሰጣትና አብሯት ተኛ፤ እርሷም አረገዘችለት። 19 ከዚያም ወደ መኖሪያዋ ተመልሳ፣ ሻሽዋን አውልቃ እንደወትሮዋ የመበለት ለብሷን ለበሰች። 20 ይሁዳ በመያዣ ስም የሰጣትን ዕቃዎች ለማስመለስ የፍየሉን ጠቦት በዓዶሎማዊ ወዳጁ እጅ ላከላት፣ እርሱ ግን ሊያገኛት አልቻለም። 21 “በኤናይም ከተማ መግቢያ ከመንገዱ ዳር የነበረች ያቺ ዝሙት አዳሪ የት ደረሰች?” ብሎ ዓዶሎማዊው ሰውዬ ጠየቀ። ሰዎቹም፣ “በዚህ አካባቢ እንደዚህ ያለች ዝሙት አዳሪ የለችም” አሉት። 22 ስለዚህ ወደ ይሁዳ ተመልሶ ሄደና፣ “ላገኛት አልቻልሁም፤ በዚያ የሚኖሩትም ሰዎች፥ ‘እንደዚህ ያለች ዝሙት አዳሪ እዚህ የለችም’ አሉኝ” ብሎ ነገረው። 23 ይሁዳም፣ “እንግዲህ መያዣውን እንደያዘች ትቅር አለዚያ መሳቂያ እንሆናለን። ለነገሩማ ይህን ፍየል ላክሁ፣ አንተም ፈልገህ አላገኘሃትም” አለ። 24 ከሦስት ወር ያህል በኋላ፣ “ምራትህ ትዕማር ዘማዊ ሆናለች፤ ከዚህም የተነሣ አርግዛለች” ተብሎ ለይሁዳ ተነገረው። ይሁዳም፣ “አውጧትና በእሳት ተቃጥላ ትሙት” አለ። 25 እርሷም ተይዛ በምትወሰድበት ጊዜ ለአማትዋ፣ “እኔ ያረገዝሁት የእነዚህ ዕቃዎች ባለቤት ከሆነ ሰው ነው” ስትል ላከችበት፤ ደግሞም፣ “የማኅተሙ ቀለበት ከነማንጠልጠያውና በትሩ የማን እንደሆነ እስቲ ተመልከት” አለችው። 26 ይሁዳም ዕቃዎቹን አውቆ፣ “ልጄ ሴሎም እንዲያገባት ባለማድረጌ፣ እርሷ ከእኔ ይልቅ ትክክል ናት” አለ። ከዚያም በኋላ ከእርሷ ጋር አልተኛም። 27 የመውለጃዋ ጊዜ እንደደረሰም ፅንሷ መንታ መሆኑ ታወቀ። 28 በምትወልድበትም ጊዜ አንደኛው እጁን አወጣ፤ አዋላጂቱም፣ “ይህኛው መጀመሪያ ወጣ” ስትል በእጁ ላይ ቀይ ክር አሰረችለት፤ 29 ነገር ግን፣ እጁን መልሶ ሲያስገባ ወንድሙ ተወለደ። አዋላጂቱም፣ “አንተ እንዴት ጥሰህ ወጣህ!” አለች፣ ከዚያም ስሙ ፋሬስ ተባለ። 30 ከዚያ በኋላ እጁ ላይ ቀይ ክር የታሰረለት ወንድሙ ተወለደ፣ ስሙም ዛራ ተባለ።



Genesis 38:1

በዚያም ወራት ይሁዳ

ይህ ስለ ይሁዳ የሚናገረውን አድስ የታሪኩን ክፍል ያስታውቃል (አድስ ክስተት መጀመር ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

ኤራስ ወደተባለ ዓዶሎማዊ

ኤራስ በዓዶሎም የሚኖር ወንድ ሰው ስም ነው (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

ሴዋ

ሴዋ ይሁዳን ያገባች ከነዓናዊ ሴት ነች (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

Genesis 38:3

እርስዋም ጸንሣ

የይሁዳ ሚስት ጸንሣ

ዔር ተብሎ ተሠየመ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “አባቱ ዔር ብሎ ሰየመው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ስሙንም … ጠራው

ሰየመው

ክዚብ

የቦታ ወይም የሀገር ስም ነው (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

Genesis 38:6

ዔር

ይህ የይሁዳ ወንድ ልጅ ስም ነው:: በዘፍጥረት 38:3 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ነበር

በእግዚአብሔር ፊት የሚለው ሀረግ እግዚአብሔር የዔርን ክፋት እንደአየው ያመለክታል:: አት: “ክፉ ነበርና እግዚአብሔር አየው” (ፊሊጣው አነጋገር ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ቀሠፈው

ክፉ ከመሆኑ የተነሣ እግዚአብሔር ቀሠፈው:: ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “ስለዚህ እግዚአብሔር ቀሠፈው” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 38:8

አውናን

ይህ ከይሁዳ ወንድ ልጆች የአንዱ ስም ነው በዘፍጥረት 38፡4 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

ወደ ወንድምህ ሚስት ግባ

ይህ ታላቅ ወንድም አግብቶ ሳለ ልጅ ሳይወልድ ቢሞት ተከታይ ወንድሙ ወደ መበለትዋ በመግባት ሩካቤ ሥጋ በመፈጸም ዘርን የማስቀጠል ባህል እንደሆነ ያመለክታል መበለትዋ የመጀመሪያ ወንድ ከወለደች ያ ወንድ ልጅ የሞተው ወንድም ልጅ እንደሆነ በመቆጠር የሟቹን ሀብት ይወርሳል::

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ነበር

በእግዚአብሔር ፊት የሚለው ሀረግ እግዚአብሔር የአውናን ክፋት እንደአየው ያመለክታል:: አት: “ክፉ ነበርና እግዚአብሔር አየው” (ፊሊጣው አነጋገር ይመልከቱ)

እንዲሁም ደግሞ እግዚአብሔር ቀሠፈው

ያደረገው ነገር ክፉ ከመሆኑ የተነሣ እግዚአብሔር ቀሠፈው:: ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “ስለዚህ እንዲሁ ደግሞ እግዚአብሔር ቀሠፈው” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 38:11

ምራቱ

የታላቅ ወንድ ልጁ ሚስት

ወደ አባትሽ ቤት

ይህም ማለት በዚህ በአባትዋ ቤት እንዲትኖር ነው:: አት “እናም በአባትሽ ቤት… ቢትኖሪ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ልጄ ሴሎም ለአካለ መጠን እስኪደርስ ድረስ

ይሁዳ ትዕማር ሴሎም ለአካለመጠን በደረሰ ጊዜ እንዲታገባው ያስባል፡፡ አት “ልጄ ሴሎም ለአካለ መጠን በደረሰ ጊዜ ሊያገባሽ ይችላል” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሴሎም

ይህ ከይሁዳ ወንድ ልጆች የአንዱ ስም ነው በዘፍጥረት 38፡5 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

እንደ ወንድሞቹ ተቀሥፎ ይሞትብኛል ብሎ ስለ ሠጋ

ሴሎም ትዕማርን ቢያገባ እንደ ወንድሞቹ ይሞትብኛል ብሎ ይሁዳ ሠግቶአል:: አት “እርሱ እርስዋን ካገባ እንደወንድሞቹ ይሞትብኛል ብሎ ስለሠጋ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 38:12

ሹዓ

ይህ የወንድ ሰው ስም ነው በዘፍጥረት 38፡2 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

ይሁዳ ከሀዘኑ ተጽናና

ይሁዳም ሀዘኑን ባቆመ ጊዜ

የበጎቹን ጸጉር ወደሚሸልቱት ሰዎች ወደ ተምና

ተምና የበጎቹንነ ጸጉም የሚሸልቱ ስዎች ወዳሉበት ሥፍራ

ተምና … ኤናይም

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

እርሱና የእርሱ ጓደኛ ዓዶላማዊው ሒራ

ከዓዶላም ጓደኛው ሒራ አብሮት ሄደ

ሒራ ዓዶላማዊው

ሒራ የወንድ ሰው ስም ነው እናም ዓዶላም እርሱ የሚኖርበት ቀበሌ ስም ነው፡፡ በዘፍረት 38፡1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ትዕማር ተነገራት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት “አንድ ሰው ለትዕማር ነገራት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እይው አማትሽ

ስሚ ፤ እዚህ “እይው” የሚለው ቃል የትዕማርን ትኩረት ለመሳብ ተጠቅሞአል፡፡

አማትሽ

የባልሽ አባት

የመበለትነት ልብስ

መበለቶች የሚለብሱት ልብስ

ሻሽ

ሴቶች ፊታቸውንና ጭንቅላታቸውን ለመሸፈን የሚጠቀሙት ከስስ ጨርስ የተሰራ ልብስ

ራስዋን ተከናንባ

ይህም ሰዎች እንዳያውቃት ራስዋን በልብስ በመከናነብ ሸፈነች ማለት ነው ሴቶች ራሳቸውን መከናነብ የሚያስችላቸው ሰፋፊ ልብሶች በባህሉ የተለመዱ ናቸው አት ሰዎች እንዳያውቃት በሰፋፊ ልብሶች ተከናነበች (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

መንገድ ዳር

በመንገድ ዳር ወይም በመንገድ

ለእርሱ ሚስት ሆና አልተሰጠችም ነበር

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ይሁዳ ለሴሎም ሚስት አድርጐ አልሰጣትም ነበር” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 38:15

ፊትዋን ስለሸፈነች

ይሁዳ እንደ ጋለሞታ ያሰባት ፊትዋን ስለሸፈነች ብቻ ሳይሆን በከተማው መግቢያም ስለተቀመጠች ነው አት ጭንቅላትዋን ስለሸፈነችና ጋለሞቶች በሚቀመጡበት ቦታ ስለተቀመጠች ነበር (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ወደ እርስዋም አዘነበለ

ትዕማር በመንገዱ ዳር ነበረች አት እርስዋም ወደተቀመጠችበት ወደ መንገዱ ዳር ሄደ ወይም አዘነበለ(ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

እባክሽ ነዪ

እባክሽ ወደ እኔ ነዪ ወይም እባክሽ አሁነ ነዪ

ምራቱ

የልጁ ሚስት

Genesis 38:17

ከመንጋዬ

ከፍዬሎች መንጋዬ

ማኀተም ቀለበት ከነማሰሪያው …. በትር

ማኀተም ብር መሣይ በላዩ ላይ ቅርጽ የተቀረጸበት የቀለጠ ሰም ለመቅረጽ የሚጠቀምበት ነው ቀለበት ማኀተም ያለበትና ባለቤቱ በአንገት የሚያደረገው ነው በትር ከረጅም እንጨት የተሠራና በአዳጋች በመንገድ የሚጠቀሙበት ነው

ለእርሱም ጸነሰች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት “እርሱም እርሷን አስረገዛት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 38:19

ሻሽ

ሴቶች ፊታቸውንና ጭንቅላታቸውን ለመሸፈን የሚጠቀሙት ከስስ ጨርስ የተሰራ ልብስ ነበር:: በዘፍጥረት 38: 14 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

የመበለት ልብስዋን ለበሰች

መበለቶች የሚለብሱትን ልብስ ለበሰች:: በዘፍጥረት 38: 14 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

አዶሎማዊ

በአዶሎም ቀበለ የሚኖር ሰው በዘፍጥረት 38፡ 1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

መያዣ የሰጣትን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት “መያዣውን ለማስመለስ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ከሴቲቱ እጅ

እዚህ እጅ የሚለው ቃል በእርስዋ ቁጥጥር ሥር እንደሆነ አበክሮት ይሰጣል:: የሴቲቱ እጅ ሴቲቱን ይወክላል:: አት “ከሴቲቱ” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 38:21

አዶሎማዊ

በአዶሎም ቀበለ የሚኖር ሰው በዘፍጥረት 38 1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የአገሩ ሰዎች

በዚያ ከሚኖሩ ሰዎች እንዳንዶች

ቤተ ጣዖት ዝሙት አደሪዋ

በቤተ ጣዖት የሚታገለግል ዝሙት አዳሪ

ኤናይም

ይህ የቦታ ስም ነው በዘፍጥረት 38፡14 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

አለዚያ መሳቂያ እንሆናለን

የሆነውን ነገር ሰዎች ከሰሙ በይሁዳ ይስቁበታል ይሣለቁበታል:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ወይም ደግሞ የሆነውን ሰዎች ካወቁ ይስቁብናል” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ እና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 38:24

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ የታሪኩን አድስ አካል ጅማሬ ያመለክታል (አድስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

ለይሁዳ ተነገረው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “አንድ ሰው ለይሁዳ ነገረው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ምራትህ ትዕማር

ትዕማር የታላቅ ልጅህ ሚስት

ከዚህም የተነሣ ጸነሰች

ከዚህ የሚለው ቃል ከዝሙት ከፈጸመችው ዝሙት ማለት ነው ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ከዚህም አረገዘች” ወይም “አረገዘች” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አምጡአት

አውጡአት

በእሳት ትቃጠል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እንዲትሞት እናቃጥላታለን” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እርስዋም ባወጡአት ጊዜ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እነርሱ ባወጡአት ጊዜ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አማትዋ

የባልዋ አባት

ማኀተም ቀለበት ከነማሰሪያው …. በትር

ማኀተም ብር መሣይ በላዩ ላይ ቅርጽ የተቀረጸበት የቀለጠ ሰም ለመቅረጽ የሚጠቀምበት ነው:: ቀለበት ማኀተም ያለበትና ባለቤቱ በአንገት የሚያደረገው ነው በትር ከረጅም እንጨት የተሠራና በአዳጋች በመንገድ የሚጠቀሙበት ነው:: (በዘፍጥረት 38: 18 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ)

ሴሎም

ይህ ከይሁዳ ወንድ ልጆች የአንዱ ስም ነው:: በዘፍጥረት 38፡5 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተረጐም ይመልከቱ)

Genesis 38:27

በዚያን ጊዜ

ይህ ሀረግ የታሪኩ አድስ ክፍል መጀመሩን ያመለክታል (አድስ ክስተት ስለማታወቅ ይመልከቱ)

እነሆ

እነሆ የሚለው ከዚህ በፊት ያልታወቀው ትዕማር መንታ ልጆችን እንደተሸከመች እንድንገረም ለማድረግ ተጠቅሞአል

ስትወልድም እንዲህ ሆነ

እንዲህ ሆነ የሚለው ሀረግ በታሪኩ ዋና ክስተት ያመለክታል በቋንቋዎ ይህን የመሰለውን የመግለጽ አባባል ካለ ይጠቀሙ

አንደኛው እጁን አወጣ

ከሕጻኖች አንደኛው እጁን አወጣ

አዋላጅ

አንድ ሴት በሚትወልድበት ጊዜ የሚረዳት ሰው ነው በዘፍረት 35:17 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

ቀይ ክር

ደማቅ ቀይ ክር

በእጁ

በአምባሩ ዙሪያ

Genesis 38:29

እነሆ

እነሆ የሚለው ቃል ለሚከተለው የሚያስገርም መረጃ ትኩረት እንድንሰጠው ነው

እንዴት ጥሰህ መጣህ!

ይህ ሁለተኛው ሕጻን ቀድም ሲወጣ አዋላጅዋ በማየት የተደነቀችውን የሚያሳይ ነው:: አት “እንዴት የራስህን መንገድ ጥሰህ ወጣህ!” ወይም “ሰንጥቀህ ቀድመህ ወጣህ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመለከቱ)

ስም ተሰጠው ወይም ተሰየመ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት “እርስዋ ስም ሰጠችው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ፋሬስ

የወንድ ልጅ ስም ነው ተርጓሚዎች እንደሚከተለው የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ:: ፋሬስ የሚለው ስም ጥሶ መውጣት ማለት ነው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዛራ

ይህ የወንድ ልጅ ስም ነው ተርጓሚዎች እንደሚከተለው የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ:: ዛራ የሚለው ስም ቀይ ክር ወይም ደማቅ ቀይ ክር ማለት ነው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)


Chapter 39

1 ዮሴፍ ወደ ግብፅ ተወስዶ ነበር፤ ከፈርዖንም ሹማምንት አንዱ የነበረውም የዘበኞች አለቃ፣ ግብፃዊው ጴጥፋራ ወደዚያ ከወሰዱት ከእስማኤላውያን ነጋዴዎች እጅ ገዛው። 2 እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር ስለነበረ ኑሮው ተቃናለት፤ እርሱም በግብፃዊው አሳዳሪው ቤት ኖረ። 3 አሳዳሪው እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር እንዳለና ሥራውንም ሁሉ እንዳከናወነለት ባየ ጊዜ፣ 4 ዮሴፍ በእርሱ ዘንድ ሞገስ አገኘ፣ የቅርብ አገልጋዩም ሆነ። ጲጥፋራ በቤቱ ላይ ሾመው፣ ያለውንም ሀብት ሁሉ በኃፊነት ሰጠው። 5 ዮሴፍ በጲጥፋራ ቤትና ባለው ሀብት ሁሉ ላይ ከተሾመበት ጊዜ ጀምሮ እግዚአብሔር የግብፅዊውን ቤት ባረከ፣ የእግዚአብሔርም በረከት በግቢም በውጭም ባለው የጲጥፋራ ሀብት ንብረት ሁሉ ላይ ሆነ። 6 ስለዚህ ጲጥፋራ ባለው ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጠው፣ የቀረበለትንም ከመመገብ በስተቀር፣ ማናቸውንም ጉዳይ በዮሴፍ ላይ ጥሎ ነበር። ዮሴፍ ጥሩ ቁመና ያለውና መልከ-መልካም ነበር፤ 7 ከጊዜ በኋላ የጌታው ሚስት ዮሴፍን ተመልክታ ስላፈቀረችው፣ “ና ከእኔ ጋር አብረን እንተኛ” አለችው። 8 እርሱ ግን ይህን ለመፈጸም ፈቃደኛ አልሆነም፤ እንዲህም አላት፤ “ጌታዬ ያለውን ሁሉ በኃላፊነት ስለሰጠኝ፣ በቤቱ ውስጥ ስላልው ሁሉ ምንም የሚያውቀው ነገር የለም። 9 በዚህ ቤት ላይ ከእኔ የበለጠ ኃላፊነት ያለው ማንም የለም፣ ከአንቺ በቀር በእኔ ቁጥጥር ሥር ያላደረገው ምንም ነገር የለም፤ ይኸውም ሚስቱ ስለሆንሽ ነው፤ ታዲያ፣ እኔ ይህን ክፉ ድርጊት በእግዚአብሔር ፊት እንዴት እፈጽማለሁ?” 10 ይህንም ነገር በየዕለቱ ለዮሴፍ ትነግረው ነበር፤ እርሱም ከእርሷ ጋር ይተኛ ዘንድ ከእርስዋም ጋር ይሆን ዘንድ አልሰማትም። 11 አንድ ቀን ዮሴፍ ለሥራ ጉዳይ ወደ ቤት ሲገባ በቤት ውስጥ አንድም ሠራተኛ አልነበረም፤ 12 እርሷም ልብሱን ጨምድዳ ይዛ፣ “በል አብረኸኝ ተኛ” አለችው። እርሱ ግን ልብሱን እጅዋ ላይ ትቶላት ከቤት ሸሽቶ ወጣ። 13 እርሷም ልብሱን በእጅዋ ላይ ትቶ ከቤት ሸሽቶ መውጣቱን በተመለከተች ጊዜ፣ 14 አገልጋዮችዋን ጠርታ እንዲህ አለቻቸው፣ “እነሆ፣ ባለቤቴ ያመጣው ይህ ዕብራዊ ሊያዋርደኝ ነበር፤ ወዳለሁበት ክፍል ገብቶ ሊደፍረኝ ሞከረ፤ እኔ ግን ድምፄን ከፍ አድርጌ ጮኽሁ። 15 ዕርዳታ ለማግኘትም መጮኼን በሰማ ጊዜ ልብሱን በአጠገቤ ትቶ ከቤት ሸሽቶ ወጣ።” 16 የዮሴፍ አሳዳሪ እስኪመጣ ድረስ ልብሱን በእርስዋ ዘንድ አቆየችው። 17 በመጣም ጊዜ የሆነውን ታሪክ እንዲህ ስትል ዘርዝራ ነገረችው፤ “አንተ ወደዚህ የመጣኸው ዕብራዊ አገልጋይ ወዳለሁበት ክፍል ገብቶ ሊያዋርደኝ ነበር። 18 ነገር ግን ድምፄን ከፍ አድርጌ በጮኽሁ ጊዜ ልብሱን በአጠገቤ ትቶ ከቤት ሸሽቶ ወጣ።” 19 “የአንተ አገልጋይ እንዲህ አደረገኝ” ብላ የነገረችውን ታሪክ በሰማ ጊዜ የዮሴፍ አሳዳሪ እጅግ ተቆጣ። 20 ዮሴፍንም ወስዶ፣ የንጉሥ እስረኞች ወደታሠሩበት እስር ቤት አስገባው። 21 እግዚአብሔር ዘላለማዊ ፍቅሩን ዐሳየው፣ በእስር ቤት አዛዡም ዘንድ ሞገስን ሰጠው። 22 ስለዚህ የእስር ቤቱ አዛዥ ዮሴፍን የእስረኞች ሁሉ አለቃ አደረገው፤ በእስር ቤት ላለውም ነገር ሁሉ ኃላፊ ሆነ። 23 እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር ሆኖ የሚያደርገው ነገር ሁሉ እንዲቃናለት ስላደረገ የእስር ቤት አዛዥ በዮሴፍ ቁጥጥር ሥር በነበረው ነገር ምንም ዐሳብ አልነበረበትም።



Genesis 39:1

ዮሴፍ ወደ ግብጽ ወርዶ ነበር

ወደ ግብጽ መጓዝ ወደ ላይ ወደ ተስፋይቱ ምድር የመጓዝ ተጻራሪ ወደ ታች መውረድ ተደርጐ ይቆጠራል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እስማኤላዊያን ዮሴፍን ወደ ግብጽ ወሰዱት” (ፈሊጣዊ አነጋገርና ተሻጋሪ ግሥ እና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እግዚአብሔር የዮሴፍ ጋር ነበረ

ይህ እግዚአብሔር ዮሴፍን ረድቶታል ሁልጊዜም ከእርሱ ጋር ነበር ማለት ነው:: አት “እግዚአብሔር ዮሴፍን መራው አገዘውም” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አሳዳሪው ቤት ኖረ

እዚህ ጸሓፊው በአሳዳሪው ቤት መሥራቱን በአሳዳሪው ቤት እንደመኖር ይናገራል:: በአሳዳሪዎቻቸው ቤት መሥራት የሚችሉት በጣም ታማኝ የሆኑ ሎሌዎች ብቻ ናቸው፡፡ አት እርሱም በቤት ውስጥ ይሠራ ነበር (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 39:3

አሳዳሪው እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር እንዳለ አየ

አሳዳሪው እግዚአብሔር እርሱን እየረዳ እንደሆነ አየ ማለት ነው አት እግዚአብሔር እየረዳው እንደሆነ አሳዳሪው አየ (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ሥራውን ሁሉ እንዳከናወነለት

እግዚአብሔር ዮሴፍ የሚሠራው ሁሉ መከናወንለት አደረገ

ዮሴፍ በእርሱ ዘንድ ሞገስ አገኘ

ሞገስ ማግኘት በአንድ ሰው ተቀባይነትን ማስረገጥ ማለት ነው በእርሱ ዘንድ የሚለው ፈሊጣዊ አባባል በሰውዬው አመለካከት እንደሆነ ያመለክታል:: ተገቢ ትርጉሞች እነሆ 1) ጲጥፋራ በዮሴፍ ተደስቶአል 2) እግዚአብሔር በዮሴፍ ተደስቶአል (ፈሊጣዊ አባባል ይመልከቱ)

ጲጥፋራን አገለገለ

የጲጥፋራ የግል ሎሌው ነበር ማለት ነው

ጲጥፋራ ዮሴፍን በቤቱ ላይ ሾመው ያለውን ሀብት ሁሉ በኃላፊነት ሰጠው

ጲጥፋራ በቤቱና የጲጥፋራ በሆነው ሁሉ ላይ ለዮሴፍ በኃላፊነት ሰጠው

በእርሱ ኃላፊነት ሥር አደረገ

አንድ ነገር በአንድ ሰው ኃላፊነት ሥር ሲሆን ያ ሰው ያንን ነገር ለመንከባከብና ደኀንነቱን ለመጠበቅ ኃላፊነት አለው ማለት ነው:: አት “ዮሴፍ እንዲንከባከብ ሰጠው” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 39:5

ዮሴፍ በጲጥፋራ ቤትና ባለው ሀብት ሁሉ ላይ ከተሾመበት ጊዜ ጀምሮ እግዚአብሔር የግብጻዊውን ቤት ባረከ

ተውላጤ ስሞችን ከመጠቀምዎ በፊት “ዮሴፍ” እና “ግብጻዊው” የሚሉ ቃላትን መጠቀም ይችላሉ:: ግብጻዊው ዮሴፍን በቤቱና ባለው ሀብት ሁሉ ላይ ኃላፊነት ሰጠው እናም ከጊዜ ወደ ጊዜ በዮሴፍ ምክንያት እግዚአብሔር የግብጻዊውን ቤት ባረከ::

እንዲህም ሆነ

እነዚህ ሁለቱ ጥቅሶች ለሚቀጥለው ክስተት ዳራ መረጃ እንደሆኑ ለአንባቢያን ለመናገር ይህ ሀረግ ተጠቅሞአል

እርሱም እርሱን በቤቱና ባለው ሀብት ሁሉ ላይ ሾመው

ጲጥፋራ ዮሴፍን በቤቱና ባለው ተብት ሁሉ ላይ ሾመው

ባረከው

በሚባረከው ነገር ወይም ሰው መልካም ወይም ጠቃሚ ነገር እንዲደረግ ምክንያት መሆን ማለት ነው

የእግዚአብሔር በረከት ሆነ

እዚህ ጸሐፊው እግዚአብሔር የሰጠውን በረከት በአንድ ነገር ላይ እንደተቀመጠ መሸፈኛ አድርጐ ይናገራል:: አት: “እግዚአብሔር ባረከ” ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ

በግቢም በውጭም ባለው የጲጥፋራ ሀብት ንብረት ሁሉ

ይህ ቤት እረሻውንና ከብቶችን ያለመክታል የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “በጲጥፋራ ቤትና በከብቶችና እርሻው ሁሉ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቀ መረጃ ይመልከቱ)

ጲጥፋራ ማንኛውንም ጉዳይ በዮሴፍ ቁጥጥር ሥር አድርጐ/በዮሴፍ ላይ ጥሎ ነበር

አንድ ነገር በአንድ ሰው ቁጥጥር ሥር ሲሆን ያ ሰው ሊጠብቀውና ሊንከባከበው ኃላፊነት አለው ማለት ነው አት: “ስለዚህ ጲጥፋራ ባለው ሁሉ ላይ ለዮሴፍ ስልጣን ሰጠው”

ከሚበላው እንጀራ በቀም ምንም የሚያውቀው አልነበረም

ምን ምግብ መመገብ እንዳለበት ከመወሰን በቀር በቤቱ ስላለው ማንኛውም ነገር አይጨነቅም ነበር ይህ በአዎንታዊ መንገድ ሊገለጽ ይችላል አት ጲጥፋራ ምን መመገብ እንደሚፈልግ ብቻ ማሰብ ነበረበት በቤቱ ስላለው ማንኛውም ነገር መጨነቅ የለበትም (ግምታዊ እውቀትና ጥልቀ መረጃ ይመልከቱ)

አሁንም

“አሁንም” የሚለው ቃል ስለ ዮሴፍ ዳራ መረጃ ለመስጠት በታሪኩ መስመር ውስጥ ጣልቃ ማስገባቱን ያመለክታል (ዳራ መረጃ ይመልከቱ)

ዮሴፍ መልከ መልካምና ውብ ነበር

ሁለቱም ቃላት ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው ዮሴፍ የሚያስደስት ቁመና እንዳለው ያመለክታሉ:: ጠንካራና ጥሩ ቁመና ነበረው:: አት: “ጠንካራና መልከመልካም ነበር”

Genesis 39:7

ከዚህ በኋላ እንደዚህ ሆነ

እናም ደግሞ ይህ ሀረግ አድስ ክስተት መጀመሩን ሊያመለክት ተጠቅሞአል (አዲስ ክስተት ማታወቅ ይመልከቱ)

እይው

ስሚው ዮሴፍ የጲጥፋራን ሚስት መስብ/ትኩረት ለማግኘት ይህን ቃል ተጠቅሞአል

ጌታዬ በቤቱ ውስጥ ስላለው ሁሉ ምንም የሚያውቀው ነገር የለም

“ጌታዬ በኃላፊነቴ ሥር ስላለው ስለቤቱ ሁሉ ምንም የሚያውቀው ነገር የለም”:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ጌታዬ ስለቤቱ ያምነኛል” (ድርብ አሉታዊነት ይመልከቱ)

ጌታዬ ያለውን ሁሉ በኃላፊነት ለእኔ ስለሰጠኝ

አንድ ነገር “በአንድ ሰው ኃላፊነት ሥር” ሲሆን ያ ሰው እንዲንከባከበውና እንዲጠብቀው ኃላፊነት አለው ማለት ነው:: አት፡ “ያለውን ሁሉ በኃላፊነት ስለሰጠኝ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ለዚህ ቤት ከእኔ የሚበልጥ ሰው የለም

እዚህ ጸሓፊው ኃላፊነትን እንደ ትልቅነት ይናገራል አት: “ከማንም ሰው የበለጠ ለዚህ ቤት ኃላፊነት አለኝ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ከአንቺ በቀር ያልሰጠኝ ነገር የለም

ይህ በአዎንታዊ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “እርሱ ያለሰጠኝ ነገር ቢኖር አንቺን ብቻ ነው” (አሉታዊነትን በአዎንታዊነት የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

እንዴት ይህን ክፉ ድርጊት ፈጽሜ በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአት እሠራለሁ

ዮሴፍ ትኩረት ለመስጠት ጥያቄ ይጠቀማል ይህ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊገለጽ ይችላል አት ይህን ክፉ ድርጊት ፈጽሜ በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአት አልሠራም (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

Genesis 39:10

በየዕለቱ ለዮሴፍ ትነግረው ነበር

ከእርስዋ ጋር እንዲተኛ በተደጋጋሚ ትጠይቀው ነበር ማለት ነው:: የዚህ ጥቅስ ሙሉ ትርጉሙ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “ዮሴፍ ከእርስዋ ጋር እንዲተኛ ትጐተጉተው ነበር” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ከእርስዋም ጋር እንዲሆን

እንዲቀርባት

እንዲህም ሆነ

“እንዲሁም ደግሞ” የሚለው ሀረግ በታሪኩ አድስ ክስተት መጀመሩን ለማመልከት ነው (አዲስ ክስተት ስለማታወቅ ይመልከቱ)

ከቤቱ አገልጋዮችም አንድም ሰው

በቤቱ ከሚያገለግሉ ሰዎች ማንም

ሸሽቶ ከቤት ወጣ

“እናም ወዲያው ሮጦ ወደ ውጪ ወጣ” ወይም “እናም ወዲያው ሮጦ ከቤት ወጣ”

Genesis 39:13

እንዲህም ሆነ …. ጠራች

ከዚያም …. ጠራች እንዲህም ሆነ የሚለው ሀረግ በታሪኩ ሁለተኛውን ክስተት ለማመልከት ተጠቅሞአል (አዲስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

ሸሽቶ ወደ ውጭ ወጣ

ወዲያው ሮጦ ከቤት ወጣ

የቤትዋን ሰዎች

በቤትዋ የሚሠሩ ሰዎች

አያችሁ

“ተመልከቱ” ወይም “ሰማችሁ” ወይም “ስለሚናገረው ነገር ትኩረት አድርጉ”

ከእኔ ጋር ሊተኛ ወደ እኔ ገባ

እዚህ የጲጥፋራ ሚስት ዮሴፍ ሊይዛትና ከእርስዋ ጋር ሊተኛ እንደሞከረ ትከሳለች

እንዲህም ሆነ መጮሄን ሲሰማ

ድምጼን ከፍ አድርጌ መጮሄን ሲሰማ እንዲህም ሆነ የሚለው ሀረግ የተጠቀመው በታሪኩ ሁለተኛውን ክስተት ለማመልከት ነው (አዲስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

Genesis 39:16

ጌታውም

የዮሴፍ ጌታ ይህ ጲጥፋራን ያመለክታል::

እንዲህ ስትል ነገረችው

ይህን ነገር እንዲህ ብላ ነገረችው

ወደ እኛ ያመጣሄው

“እኛ” የሚለው ቃል ጲጥፋራን ሚስቱንና ሌሎች በቤት ውስጥ ያሉትን ጠቃልላል (ሁሉ አቀፍ እኛን ይመልከቱ)

መሣለቂያ ሊያደርገኝ ወደ እኔ ገባ

መሣቂያ ሊያደርገኝ ወደ እኔ ገባ መሣለቂያ የሚለው ቃል ሊይዘኝና ከእኔ ጋር ሊተኛ የሚለውን አባባል በንኀብነት ወይም አንድን ነገር ለዘብ ባለ በተዘዋዋሪ መንገድ የሚገለጽ ነው:: አት “ወዳለሁበት ገባ አስገድዶ ከእኔ ጋር ሊተኛ ሞከረ” (ንኀብነት ወይም አንድን ነገር ለዘብ ባለ በተዘዋዋሪ መንገድ የሚገለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

እንዲህም ሆነ

“ከዚያም” የጲጥፋራ ሚስት ይህን ሀረግ የተጠቀመችው ዮሴፍ ከእርስዋ ጋር ለመተኛት መሞከሩን ለእርሱ የሚትነግረውን የታሪኩን ሁለተኛውን ክስተት ለማመልከት ነው::(አዲስ ክስተት ስለማታወቅ ይመልከቱ)

ሸሽቶ ወደ ውጭ ወጣ

ወዲያው ሮጦ ከቤት ወጣ

Genesis 39:19

እንዲህም ሆነ

“እንዲህም ሆነ” የሚለው ሀረግ በታሪኩ አዲስ ክስተት መጀመሩን ለማመልከት ተጠቅሞአል (አዲስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

ጌታውም

የዮሴፍ ጌታ ይህ ጲጥፋራን ያመለክታል ይህ መረጃ ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት የዮሴፍ ጌታ ጲጥፋራ

እጅግ ተቈጣ

ጲጥፋራ እጅግ ተቈጣ

የንጉሡ እስረኞች ወደ ተጋዙበት እስር ቤት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አተ ንጉሡ እስረኞችን ያኖረበት ቦታ ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ

በዚያ ነበረ

ዮሴፍ በዚያ ቆየ

Genesis 39:21

ነገር ግን እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር ነበረ

እግዚአብሔር ለዮሴፍ ተጠነቀቀለት እናም ቸር ነበረ:: “ነገር ግን እግዚአብሔር ለዮሴፍ ቸር ነበር” ወይም “እግዚአብሔር ዮሴፍን ተንከባከበ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የቃል ኪዳን ታማኝነቱን ገለጸለት

“ታማኝነት” የሚለው ረቂቅ ስም “ታማኝ” ወይም “በታማኝነት” ሊገለጽ ይችላል:: አት ከእርሱ ጋር ለገባው ቃል ኪዳን ታማኝ ነበር ወይም በታማኝነት ወደደው (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

በወህኑ ቤት አዛዡም ዘንድ ሞገስን ሰጠው

ይህም እግዚአብሔር የወህኑ ቤት አዛዥ ዮሴፍን እንዲቀበለውና እንዲንከባከበው አደረገው አት እግዚአብሔር የእስር ቤቱ አዛዥ በዮሴፍ እንዲደሰት አደረገው (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የእስር ቤቱ አዛዥ

“የእስረኞች አስተዳደር” ወይም “በእስር ቤቱ ኃላፊነት የተሰጠው”

በዮሴፍ እጅ አሳልፎ ሰጣቸው

እዚህ “እጅ” የሚለው የዮሴፍን ኃይል/አቅም ወይም ታማኝ ኃላፊነት ይወክላል”” አት “ዮሴፍን አለቃ አደረገው” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በዚያ ለሚደረገው ማንኛውም ነገር ዮሴፍ ኃላፊ ነበር

“ዮሴፍ በዚያ ለሚደረገው ነገር ሁሉ ኃላፊ ነበር”

እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ስለነበረ

ይህ እግዚአብሔር እንዴት እንደረዳውና እንደመራው የሚያመለክት ነው፡፡ አት “እግዚአብሔር ዮሴፍን ስለመራው” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የሚያደርገውን ሁሉ እግዚአብሔር ያሳካለት ነበር

ዮሴፍ የሚያደርገውን ሁሉ እግዚአብሔር ያሳካለት ነበር


Chapter 40

1 ከዚህም በኋላ የግብፅ ንጉሥ የመጠጥ አሳላፊውና የእንጀራ ቤት ኃላፊው ንጉሡን የሚያሳዝን በደል ፈጸሙ። 2 ፈርዖንም በመጠጥ አሳላፊዎቹ አለቃና በእንጀራ ቤቱ አዛዡ፣ በሁለቱም ሹማምንቱ ላይ እጅግ ተቆጣ፤ 3 በዘበኞቹ አለቃ ቤት ወዳለው ዮሴፍ ወደታሠረበት እስር ቤት አስገባቸው። 4 የዘበኞቹም አለቃ እስረኞቹን ለዮሴፍ አስረከባቸው፤ በእስር ቤትም ለጥቂት ጊዜ ቆዩ። 5 ታስረው የነበሩት የግብፅ ንጉሥ የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃና የእንጀራ ቤቱ አዛዥ፣ በአንድ ሌሊት የየራሳቸውን ሕልም ዐዩ፤ የሁለቱም ሕልም ለየራሱ የተለየ ፍቺ ነበረው። 6 በማግስቱ ጥዋት ዮሴፍ እነርሱ ወዳሉበት ክፍል በገባ ጊዜ ተክዘው አገኛቸውና፤ 7 “ዛሬ በፊታችሁ ላይ ሐዘን የሚታየው ለምንድን ነው?” አላቸው። 8 እነርሱም፣ “ሁለታችንም ሕልም ዐየን፤ ነገር ግን የሚተረጉምልን ሰው አጣን” ሲሉ መለሱለት። ዮሴፍም፣ “ሕልም የመተርጎም ችሎታ የሚሰጥ እግዝአብሔር ነው፣ ስለዚህ የእያንዳንዳችሁን ሕልም ንገሩኝ” አላቸው። 9 ስለዚህ የመጠጥ አሳላፊዎቹ አለቃ እንዲህ ሲል ሕልሙን ለዮሴፍ ነገረው፤ “ከፊት ለፊቴ አንዲት የወይን ተክል ዐየሁ፤ 10 ተክሏም ሦስት ሐረጎች ነበሯት፤ ወዲያው እቆጥቁጣ አበበች፤ የወይን ዘለላውም ወዲያው በሰለ። 11 የፈርዖንንም ጽዋ ይዤ ነበር፣ የወይኑን ፍሬ ለቅሜ በጽዋው ውስጥ ጨምቄ ጽዋውን በእጁ ሰጠሁት።” 12 ዮሴፍም እንዲህ አለው፤ “እንግዲህ የሕልሙ ትርጓሜ ይህ ነው፤ ሦስቱ ሐረግ ሦስት ቀን ነው፤ 13 በሦስት ቀን ውስጥ ፈርዖን ከእስር ቤት ያወጣሃል፣ ወደ ቀድሞ ሹመትህም ይመልስሃል፤ በፊት የመጠጥ አሳላፊ በነበርህበት ጊዜ ታደርግ እንደነበረው ኡሉ የፈርዖንን ጽዋ በእጁ ትሰጠዋለህ። 14 እንግዲህ፣ በጎ ነገር በገጠመህ ጊዜ፣ እኔን አስበህ ቸርነት አድርግልኝ፣ ስለ እኔም ለፈርዖን ንገርልኝ፤ ከዚህም እስር ቤት አስወጣኝ፤ 15 ከዕብራውያን ምድር ወደዚህ የመጣሁት በአፈና ነው፤ አሁንም ቢሆን እዚህ እስር ቤት የተጣልሁት አንዳች ጥፋት ኖሮብኝ አይደለም።” 16 የእንጀራ ቤት አዛዡም፣ ለመጠጥ አሳላፊዎቹ አለቃ ሕልም የተሰጠው ፍቺ ደስ የሚያሰኝ መሆኑን ሲሰማ፣ የራሱን ሕልም ለዮሴፍ እንዲህ ሲል ነገረው፤ “እኔም ደግሞ ሕልም አይቻለሁ፣ ሦስት መሶቦች በራሴ ላይ ተሸክሜ ነበር፤ 17 በላይኛው መሶብ ውስጥ ለፈርዖን የተዘጋጀ የተለያየ ምግብ ነበረበት፣ ነገር ግን ወፎች ምግቡን ከመሶቡ እያነሱ የበሉት ነበር።” 18 ዮሴፍም እንዲህ ሲል መለሰለት፤ “የሕልሙ ፍቺ ይህ ነው፤ ሦስቱ መሶብ ሦስት ቀን ነው፤ 19 በሦስት ቀን ውስጥ ፈርዖን ራስህን ካስቆረጠ በኋላ በእንጨት ላይ ይሰቅልሃል፤ ወፎችም ሥጋህን የበሉታል።” 20 በሦስተኛው ቀን የፈርዖን ልደት በዓል ስለነበር ለመኳንንቱ ሁሉ ግብዣ አደረገ፤ በዚያኑ ዕለትም የመጠጥ አሳላፊዎቹን አለቃና የእንጀራ ቤት አዛዡን ሹማምንቱ ካሉበት ከእስር ቤት አወጣቸው። 21 የመጠጥ አሳላፊዎቹን አለቃ ወደ ቀድሞ ሹመቱ መለሰው፤ እርሱም እንደ ቀድሞው ጽዋውን ለፈርዖን በእጁ ይሰጠው ጀመር፤ 22 የእንጀራ ቤት አዛዡን ግን ልክ ዮሴፍ እንደተረጎመላቸው ሰቀለው። 23 የሆነው ሆኖ፣ የመጠጥ አሳላፊዎቹ አለቃ ዮሴፍን አላስታወሰውም፤ ረሳው።



Genesis 40:1

ከዚህም በኋላ

ይህ ሀረግ የተጠቀመው በታሪኩ አዲስ ክስተት መጀመሩን ለማመልከት ነው፡፡ (አዲስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

የመጠጥ አሳላፊ

ይህ ለንጉሡ መጠጥ የሚያቀርብ ሰው ነው

እንጀራ ቤቱ

ይህ ለንጉሡ ምግብ የሚያዘጋጅ ሰው ነው

ጌታቸውን በደሉት

ጌታቸውን አስቆጡት

የመጠጥ አሳላፊዎቹ አለቃና የእንጀራ ቤቱ አዛዥ

ዋና የመጠጥ አሳላፊና ዋና እንጀራ እቅራቢ

በዘበኞቹ አለቃ ቤት ወዳለው እስር ቤት አስገባቸው

በዘበኞቹ አለቃ በሚተዳደረው የቤት ውስጥ እስር ቤት አስገባቸው

አስገባቸው

ንጉሡ ወደ እሥር ቤት አላስገባቸውም ነገር ግን እንዲታሠሩ አዘዛቸው፡፡ አት “እነርሱ እንዲያስገቡ አደረጋቸው” ወይም “ዘበኛው እንዲያስገባቸው አዘዘ” (ተዛማጅ ምትክ አባባሎችን የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ዮሴፍ ወደጋዘበት እስር ቤት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት ይህ ዮሴፍ የነበረበት ተመሣሣይ እስር ቤት ነው ወይም ይህ ጲጥፋራ ዮሴፍን ያስገባበት ተመሣሣይ እስር ቤት ነው (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 40:4

በእስር ቤት ጥቂት ጊዜ ቆዩ

በእስር ቤት አያለ ጊዜያት ቀን ተቀመጡ

Genesis 40:6

ዮሴፍ ወደእነርሱ ገባ

ዮሴፍ ወደ መጠጥ አሳላፊውና እንጀራ አቅራቢው ገባ

እነሆም አዝነው አያቸው

እነሆም የሚለው ቃል ባየው ነገር ዮሴፍ እንዴት እንደተገረመ የሚያሳይ ነው:: አት “እነርሱን አዝነው በማየቱ ተገረመ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አብረውት የነበሩ የፈርዖን ሹማምንት

ይህ የጠጅ አሳላፊዎች አለቃና የእንጀራ አቅራቢዎች አዛዥ ያመለክታል

በጌታው ግቢ በግዞት

በጌታው ግቢ በእስር ቤት፤ ጌታው የዮሴፍ ጌታ፤ የዘበኞች አለቃ የሚያመለክት ነው

ትርጓሜ ከእግዚአብሔር የማገኝ አይደለምን?

አጽንዖት ለመስጠት ዮሴፍ ጥያቄ ይመለከታል:: ይህ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ትርጓሜ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው! ወይም ለሕልሞች ትርጉምን መስጠት የሚችል እግዚአብሔር ነው” (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

እስቲ ንገሩኝ

ሕልማቸውን እንዲነግሩት ዮሴፍ ይጠይቃቸዋል:: አት “ሕልሞቻችሁን እባካችሁ ንገሩኝ”

Genesis 40:9

የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ

ለንጉሡ መጠጦችን የሚያቀርብ ዋና ሰው ነው”” በዘፍጥረት 4ዐ: 2 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

በሕልሜ እንሆ የወይን ዛፍ በፊቴ ሆና አየሁ

“በሕልሜ የወይን ጣፍ በፋቴ ሆና አየሁ!” የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ባየው ነገር እንደተደነቀና ዮሴፍ ትኩረት እንዲሰጠው ለማሳየት “እነሆ” የሚለውን ቃል ይጠቀማል::

ዘለላዎችዋም በሰሉ

ዘለላዎችዋም ተንዠርግገው በሰሉ

ጨመቅሁአቸው

ከእነዚያ የጁስ ጭማቂ አወጣሁ ማለት ነው አት ከእነዚያ ጁስ ጨምቄ አወጣሁ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 40:12

የዚህ ትርጓሜ ይህ ነው

የሕልሙ ትርጓሜ ይህ ነው

ሶስቱ ሐረግ ሶስት ቀን ነው

ሶስት ሐረጐች ሶስት ቀኖች ያመለክታሉ

በሶስት ቀኖች ውስጥ

እስከ ሶስት ቀኖች

ራስህን ከፍ ከፍ ያደርጋል

እዚህ ፊርዖን ከእስር ቤት የመጠጥ አሳላፊዎችን አለቃ የሚያወጣው ፈርዖን ከፍ ከፍ እንደሚያደርገው ተደርጐ ተነግሮአል:: አት “ከእስር ቤት ያወጣሃል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ወደ ቀድሞ ሹመትህ ይመልስሃል

ወደ ሥራህ ይመልስሃል

በነበርህበት ጊዜ

በነበርህበት ጊዜ ታደርግ እንደነበረው

Genesis 40:14

ቸርነት አድርግልኝ

ቸር ሁንልኝ

ስለእኔም ለፈርዖን ንገርልኝና ከዚህም እስር ቤት አስወጣኝ

ዮሴፍም የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ስለእርሱ ለፈርዖን እንዲነግረው ከዚህም የተነሣ ፈርዖን ከእስር ቤት እንዲያስወጣው ማለት ነው:: አት: “ስለእኔ ለፈርዖን በመንገር ከእስር ቤት እንዲወጣ እርዳኝ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በእርግጥ በአፈና ውስጥ ነኝ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “በእርግጥ ሰዎች አፍነው እምጥተውኛል” ወይም “በእርግጥ እስማኤላዊያን ይዘው አምጥተውኛል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ከዕብራዊያን ምድር

ዕብራዊ ሰዎች ከሚኖሩበት ምድር

አሁንም ቢሆን እዚህ እስር ቤት የተጣልሁት አንዳች ጥፋት ኖሮብኝ አይደለም

እናም ደግሞ እዚህ በግብጽ በሚርበት ጊዜ በእስር ቤት እንዲጣል የሚያደርገኝን ምንም ነገር አላደረግሁም

Genesis 40:16

የእንጀራ ቤት አዛዡም

ይህ ለንጉሡ ምግብ የሚያቀርብ መሪ ሰው እንደሆነ ያመለክታል:: በዘፍጥረት 4ዐ:2 ይህ እንዴት እንደተተረጐመ ይመልከቱ::

እኔም ደግሞ ሕልም አይቻለሁ እናም

እኔም ደግሞ ሕልም አይቻለሁ እናም በሕልሜ

እነሆም ሶስት መሶብ እንጀራ በራሴ ላይ ተሸክሜ ነበር

ሶስተ መሶብ እንጀራ በራሴ ላይ ተሽክሜ ነበር! እዚህ የእንጀራ ቤቱ አዛዥ “እነሆ” የሚለውን ቃል የሚጠቀመው ባየው ሕልም መገረሙንና ዮሴፍም ትኩረት እንዲሰጠው ለማሳየት ነው::

ለፈርዖን ከተዘጋጀው እንጀራ

ለፈርዖን ከተዘጋጀው ምግብ

Genesis 40:18

ፍቺው ይህ ነው

የሕልሙ ትርጉም ይህ ነው

ሶስቱ መሶቦች ሶስት ቀኖች ናቸው

ሶስት መሶቦች ሶስት ቀኖችን ይወክላሉ

ራስህን ከፍ ያደርጋል

ዮሴፍ በዘፍረት 4ዐ:13 ለመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ በሚናገርበት ጊዜ ደግሞ ራስህን ከፍ ያደርጋል የሚለውን ሀረግ ተጠቅሞአል እዚህ ግን የተለየ ትርጉም አለው አማራጭ ተገቢ ትርጉሞች: (1) በአንገትህ ገመድ በማሠር ራስህን ከፍ ያደርጋል ወይም (2) ራስህን በመቁረጥ ከፍ ያደርግሃል::

ሥጋ

የ “ሥጋ” ቀጥታ ትርጉሙ የአንድ ሰው አካል ክፍል ማለት ነው

Genesis 40:20

እንዲህም ሆነ በሶስተኛውም ቀን

ከዚያም በኋላ በሶስተኛውም ቀን እዚህ እንዲህም ሆነ የሚለው ሀረግ የተጠቀመው አዲስ ክስተትን ለማመልከት ነው (አዲስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

ግብር አበላ

ግብዣ ነበረው

የመጠጥ አሳላፊዎችን አለቃ

ይህ ለንጉሡ መጠጥን የሚያዘጋጅና የሚያቀርብ መሪ ሰው ነበር፡፡ በዘፍጥረት 4ዐ፡2 እነዚህ ቃላት እንዴት እንደተተረጐሙ ይመልከቱ፡

የእንጀራ ቤት አዛዡን

ይህ ለንጉሡ ምግብን የሚያዘጋጅ መሪ ሰው እንደሆነ ያመለክታል:: በዘፍጥረት 4ዐ:2 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

የመጠጥ አሳላፊዎቹን አለቃ ወደ ቀድሞ ሹመቱ መለሰው

የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ሹመት ወይም ኃላፊነት እንደመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ሥራው እንደሆነ ያመለክታል አት ለመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ሥራውን መልሶ ሰጠው (ተዛማጅ ምትክ ቃላትን ስለመጠቀም ይመልከቱ)

ነገር ግን የእንጀራ ቤት አዛዡን ሰቀለው

ፈርዖን ራሱ አልሰቀለውም ይሁን እንጂ እንዲሰቀል አዘዘ አት የእንጀራ ቤት አዛዥ እንዲሰቀል አዘዘ ወይም ዘበኞቹ ወይም ጥበቃዎቹ የእንጀራ ቤት አዛዡን እንዲሰቅሉ አዘዘ (ተዛማጅ ምትክ ቃላትን ስለመጠቀም ይመልከቱ)

ልክ ዮሴፍ እንደተረጐመላቸው

ይህ ዮሴፍ ሕልማቸውን እንደተረጐመላቸው የሚለውን ያመለክታል አት የሁለቱን ሰዎች ሕልም ዮሴፍ እንደተረጐመላቸው እንዲሁ ሆነ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)


Chapter 41

1 ድፍን ሁለት ዓመት ካለፈ በኋላ ፈርዖን ሕልም ዐለም፤ ሕልሙም በዓባይ ወንዝ ዳር ቆሞ ነበር፤ 2 እነሆ፣ መልካቸው ያማረ፣ ሥጋቸው የወፈረ ሰባት ላሞች ከወንዙ ወጥተው በወንዙ ዳር የበቀለውን ሣር ይበሉ ጀመር። 3 ቀጥሎም መልካቸው የከፋ አጥንታቸው የወጣ ሌሎች ሰባት ላሞች ከወንዙ ወጥተው አስቀድመው ከወጡት ላሞች አጠገብ ቆሙ። 4 እነዚህ መልካቸው የከፋና አጥንታቸው የወጣ ላሞች፥ እነዚያን ያማሩና የወፈሩ ላሞች ሲውጡአቸው ዐየ፤ ከዚያም ፈርዖን ከእንቅልፉ ነቃ። 5 ፈርዖንም እንደገና እንቅልፍ ወስዶት ሳለ ሌላ ሕልም ዐየ። በሕልሙም በአንድ የእህል አገዳ ላይ ሰባት የዳበሩና ያማሩ የእሸት ዛላዎች ዐየ፤ 6 ቀጥሎም የቀጨጩና ከበረሐ በተነሣ የምሥራቅ ነፋስ ተመትተው የደረቁ ሰባት የእሸት ዛላዎች ወጡ። 7 የቀጨጩት የእሸት ዛላዎች፤ ሰባቱን የዳበሩና ያማሩ የእሸት ዛላዎች ዋጡአቸው፤ በዚህ ጊዜ ፈርዖን ከእንቅልፉ ነቃ፣ ነገሩ ሕልም ነበር። 8 በነጋታውም ፈርዖን መንፈሱ ታወከበት፣ ስለዚህ በግብፅ አገር ያሉትን አስማተኞችና ጥበበኞች በሙሉ አስጠርቶ ሕልሞቹን ነገራቸው፣ ይሁን እንጂ፣ ሕልሞቹን ሊተረጉምለት የቻለ አንድም ሰው አልተገኘም። 9 በዚያን ጊዜ የመጠጥ አሳላፊዎቹ አለቃ ፈርዖንን እንዲህ አለው፤ “የሠራሁት በደል ዛሬ ታወሰኝ። 10 ፈርዖን ሆይ! አንተ በእኔና በእንጀራ ቤት ኃላፊው ላይ ተቆጥተህ በዘበኞች አለቃ ቤት እንድንታሰር አድርገህ ነበር፤ 11 በዚያ ሳለን በአንድ ሌሊት ሁለታችንም የተለያየ ሕልም ዐየን፤ የእያንዳንዳችንም ሕልም የተለያየ ትርጉም ነበረው። 12 በዚያን ጊዜ የዘበኞች አለቃ አገልጋይ የሆን አንድ ዕብራዊ ወጣት ከእኛ ጋር እስር ቤት ነበር። ሕልማችንን በነገርነው ጊዜ፣ ፍቺውን ነገረን፤ ለእያንዳንዳችንም እንደ ሕልማችን ተረጎመልን፤ 13 ነገሩም ልክ እርሱ እንደተረጎመልን፤ እኔ ወደ ቀድሞ ሹመቴ ተመለስሁ፤ የእንጀራ ቤት አዛዡም ተሰቀለ። 14 ፈርዖን ዮሴፍን እንዲያመጡት ትዕዛዝ ሰጠ፤ ከእስር ቤትም በጥድፊያ ይዘውት መጡ፤ ጠጉሩንም ከተላጨና ልብሱን ከለወጠ በኋላ ፈርዖን ፊት ቀረበ 15 ፈርዖንም ዮሴፍን፣ “ሕልም ዐይቼ ነበር፣ ሕልሜን ሊተረጉምልኝ የቻለ አንድም ሰው አልተገኘም፣ አንተ ግን ሕልም ሲነገርህ የመተርጎም ችሎታ እንዳለህ ሰማሁ” አለው። 16 ዮሴፍም ለፈርዖን እንዲህ ብሎ መለሰ፦ “ይህ በእኔ አይደለም፤ እግዚአብሔር ግን ለፈርዖን በበጎነት ይመልስለታል” 17 ፈርዖን ዮሴፍን እንዲህ አለው፤ “ሕልሜ በዓባይ ወንዝ ዳር ቆሜ ነበር። 18 ሥጋቸው የወፈረና መልካቸው የማረ ሰባት ላሞች ከወንዙ ወጥተው በወንዙ ዳር የበቀለውን ሣር ሲበሉ ዐየሁ። 19 ከእነርሱም በኋላ ዐቅመ ደካማ፣ መልካቸው እጅግ የከፋና አጥንታቸው የወጣ ሌሎች ሰባት ላሞች ወጡ፤ እነዚያን የመሰሉ የሚያስከፋ መልክ ያላቸው ላሞች በግብፅ ምድር ከቶ ዐይቼ አላውቅም። 20 አጥንታቸው የወጣና አስከፊ መልክ ያላቸው ላሞች መጀመሪያ የወጡትን፣ ሥጋቸው የወፈረውን ሰባቱን ላሞች ዋጧቸው። 21 ከዋጧቸውም በኋላ፣ ያው የበፊቱ መልካቸው ስላልተለወጠ እንደዋጧቸው ማንም ሊያውቅ አይችልም ነበር፤ ከዚያም ከእንቅልፌ ነቃሁ 22 ደግሞም በአንድ የእህል አገዳ ላይ ሰባት የዳበሩና ያማሩ የእሸት ዛላዎች ዐየሁ፤ 23 ቀጥሎም የቀጨጩና የደረቁ ሌሎች ሰባት ዛላዎች ወጡ። 24 የቀጨጩት የእሸት ዛላዎችም ሰባቱን ያማሩ የእሸት ዛላዎች ዋጧቸው፤ ያየኋቸውንም ሕልሞች ለአስማተኞች ነገርሁ፣ ነገር ግን ሕልሞቹን ማንም ሊተረጉምልኝ አልቻለም።” 25 ዮሴፍም ለፈርዖን እንዲህ አለው፤ “ሁለቱም የፈርዖን ሕልሞች ተመሳሳይና አንድ ዓይነት ናቸው፤ እግዚአብሔር ወደፊት የሚያደርገውን ለፈርዖን ገልጦለታል። 26 ሰባቱ የሚያምሩ ላሞች ሰባት ዓመታት ናቸው፣ ሰባቱም የሚያማምሩ የእሸት ዛላዎች ሰባት ዓመታት ናቸው፤ ሕልሙም አንድና ተመሳሳይ ነው። 27 ከእነርሱም በኋላ አጥንታቸው የወጣ አስከፊ መልክ ያላቸው ሰባት ላሞች፣ ሰባት ዓመታት ናቸው፤ እንደዚሁም ፍሬ አልባ የሆኑትና በምሥራቅ ነፋስ ተመትተው የደረቁት ሰባት የእሸት ዛላዎች ሰባት የራብ ዓመታት ናቸው። 28 አስቀድሜ ለፈርዖን እንደተናገርሁት እግዚአብሔር ወደፊት የሚያደርገውን ነገር ለፈርዖን ገልጦለታል። 29 በመላው የግብፅ ምድር እጅግ የተትረፈረፈ ጥጋብ የሚሆንባቸው ሰባት ዓመታት ይመጣሉ። 30 በዚህ በኋላ ግን በተከታታይ ሰባት የራብ ዓመታት ይሆናሉ። የራቡ ዘመን አገሪቱን እጅግ ስለሚጎዳት በግብፅ የነበረው ያለፈው የጥጋብ ዘመን ሁሉ ጨርሶ አይታወስም። 31 ከጥጋብ ዓመታት በኋላ የሚመጣው የራብ ዘመን እጅግ ጽኑ ከመሆኑ የተነሣ፣ ቀደም ሲል የነበረው የጥጋብ ዘመን ፈጽሞ ይረሳል። 32 ሕልሙ ለፈርዖን በድጋሚ መታየቱ፣ ነገሩ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቆረጠ ስለሆነ ነው፤ ይህንንም እግዚአብሔር በቅርብ ጊዜ ይፈጽመዋል፤ 33 እንግዲህ ፈርዖን ብልኅና አስተዋይ ሰው ፈልጎ፣ በመላው የግብፅ ምድር ላይ አሁኑኑ ይሹም። 34 እንደዚሁም በሰባቱ የጥጋብ ዓመታት ከሚገኘው ምርት፣ አንድ አምስተኛው እንዲሰበሰብ የሚያደርጉ ኃላፊዎችን ይሹም። 35 እነርሱም በሚመጡት የጥጋብ ዓመታት ከሚገኘው ምርት ሁሉ ይሰብስቡ፤ በፈርዖንም ሥልጣን ሥር ያከማቹ፤ ለምግብ እንዲሆኑም በየከተማው ይጠበቁ። 36 የሚከማቸው እህል፣ ወደፊት በግብፅ አገር ላይ ለሚመጣው የሰባት ዓመት ራብ መጠባበቂያ ይሁን፤ በዚህም ሁኔታ አገሪቱ በራብ አትጠፋም። 37 ዕቅዱም ፈርዖንና ሹማምንቱ ሁሉ መልካም ሆኖ አገኙት። 38 ፈርዖንም፣ “የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት እንደዚህ ያለ ሰው ልናገኝ እንችላለን?” ብሎ ጠየቃቸው። 39 ፈርዖን ዮሴፍን እንዲህ አለው፣ “እግዚአብሔር ይህን ሁል ገለጠለህ እንዳንተ ያለ አስተዋይና ብልህ ሰው የለም። 40 አንተ በቤተ መንግሥቴ የበላይ ትሆናለህ፤ ሕዝቤም ሁሉ ለሥልጣንህ ይገዛል፤ እኔ ከአንተ የምበልጠው በዙፋኔ ብቻ ይሆናል።” 41 ከዚያም፣ ፈርዖን ዮሴፍን፣ “በመላይቱ የግብፅ ምድር ላይ ኃላፊ አድርጌሃለሁ” አለው። 42 ፈርዖንም ባለማኅተሙን ቀለበት ከጣቱ አውልቆ በዮሴፍ ጣት ላይ አደረገው፤ እንዲሁም ከጥሩ የተልባ እግር የተሠራ ልብስ አለበሰው፤ በአንገቱም የወርቅ ሐብል አጠለቀለት። 43 በማዕረግ ከእርሱ ሁለተኛ ሰው አድርጎ በሠረገላ ላይ አስቀመጠው። ሰዎችም በፊቱ፣ “እጅ ንሡ” እያሉ ይጮኹ ነበር፤ በዚህ ሁኔታም በግብፅ ምድር ሁሉ ላይ ሾመው። 44 ከዝህ በኋላ ፈርዖን ዮሴፍን፣ “እኔ ፈርዖን ነኝ፤ ሆኖም በመላይቱ ግብፅ ያለ አንተ ፈቃድ ማንም ሰው እጁን ወይም እግሩን ማንቀሳቀስ አይችልም” አለው። 45 ፈርዖን ዮሴፍን ጸፍናት ፐዕናህ ብሎ ስም አወጣለት። እንዲሁም አስናት ተብላ የምትጠራውን ኦን ተብሎ የሚጠራው ከተማ ካህን የጶጢፌራን ልጅ በሚስትነት ሰጠው። 46 ዮሴፍ የግብፅ ንጉሥ ፈርዖንን ማገልገል ሲጀምር፣ ዕድሜው ሠላሳ ዓመት ነበር። ዮሴፍም ከፈርዖን ፊት ወጥቶ የግብፅን ምድር በሙሉ ዞረ። 47 በሰባቱም የጥጋብ ዓመታት ምድሪቱ የተትረፈረፈ ሰብል ሰጠች። 48 በእነዚያ ሰባት የጥጋብ ዓመታት፣ ዮሴፍ በግብፅ አገር የተገኘውን ምርት ሰብስቦ በየከተሞቹ አከማቸ፣ በእያንዳንዱ ከተማ ከየአቅራቢያው የተመረተውን እህል እንዲከማች አደረገ። 49 ዮሴፍ ብዛቱ እንደ ባሕር አሸዋ የሚሆን የእህል ሰብል አከማቸ፤ ሰብሉ እጅግ ከመብዛቱ የተነሣ ልኩን መስፈርና መመዝገብ አልቻለም ነበር። 50 ሰባቱ የራብ ዓመታት ከመምጣታቸው በፊት የኦን ከተማ ካህን የጶጢፌራ ልጅ አስናት ለዮሴፍ ሁለት ወንድ ልጆች ወለደችለት። 51 ዮሴፍም፣ “እግዚአብሔር መከራዬን ሁሉ የአባቴንም ቤት እንድረሳ አድርጎኛል” በማለት የመጀመሪያ ልጁን ስም ምናሴ አለው። 52 እንደዚሁም “መከራ በተቀበልሁበት ምድር እግዚአብሔር ፍሬያማ አደረገኝ” ሲል ሁለተኛ ልጁን ኤፍሬም አለው። 53 በግብፅ ምድር የነበረው ሰባቱ የጥጋብ ዘመን አለፈና 54 ዮሴፍ አስቀድሞ እንደተናገረው የሰባቱ ዓመት የራብ ዘመን ጀመረ። ሌሎች አገሮች ሁሉ ሲራቡ፣ በመላው የግብፅ ምድር መስፋፋት ሲጀመር፣ 55 ሕዝቡ ምግብ ይሰጠን በማለት ወደ ፈርዖን ጮኸ። ፍርዖንም ግብፃውያኑን፣ “ወደ ዮሴፍ ሂዱና የሚላችሁን አድርጉ” አላቸው። 56 ራቡ በአገሩ ላይ እየተስፋፋ ስለሄደ፣ ዮሴፍ ጎተራዎቹን ከፍቶ እህሉ ለግብፃውያን እንዲሸጥ አደረገ፤ ምክንያቱም ራቡ በመላይቱ ግብፅ ጸንቶ ነበር። 57 ራቡ በመላው ዓለም ጸንቶ ስለነበር፣ የየአገሩ ሰዎች ሁሉ ከዮሴፍ ዘንድ እህል ለመሸመት ወደ ግብፅ ምድር መጡ።



Genesis 41:1

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ የታሪኩ አድስ ክፍል መጀመሩን ያመለክታል በቋንቋዎ ይህን የሚገልጹበት መንገድ ካለ ያን ሊጠቀሙ ይችላሉ (አዲስ ክስተትን ማስታወቅ ይመልከቱ)

ድፍን ሁለት ዓመታት ካለፈ በኋላ

በእስር ቤት ከዮሴፍ አብረውት ስለነበሩት የፈርዖን መጠጥ አሳላፊዎች አለቃና እንጀራ ቤት አዛዥ ሕልሞችን ዮሴፍ ከተረጐመላቸው ሁለት ዓመታት ካለፊ በኋላ

እነሆም ቆሞ ነበር

እዚህ እነሆ የሚለው ቃል በሰፊው ታሪክ ሌላ ክስተት መጀመሩን ያመለክታል በቋንቋዎ ይህን የሚገልጹበት መንገድ ሊኖር ይችላል፡፡ አት “ቆሞ በመገኘቱ ገርሞት ነበር”

ቆሞ ነበር

ፈርዖ ቆሞ ነበር

መልካምና የወፈሩ

ጤናማና የወፈሩ

በውሃውም ዳር ባለው ቀጠማ ተሰማርተው ነበር

በወንዙ ዳር የበቀለውን ሣር ይበሉ ነበር

ቀጤማ

በረግረጋማ ቦታ የሚበቅል ቀጭንና ረጅም ሣር ነው

እነሆ ሌሎች ሰባት ላሞች

እዚህ እነሆ የሚለው ቃል ፈረዖን እንደገና ባየው ነገር እንደተገረመ ያሳያል

የከፉና የከሱ

ታማሚና የከሱ

ወንዝ ዳር

“በወንዝ ዳር” ወይም “ወንዝ ዳረቻ ላይ” ይህ በአንድ ወንዝ ዳር ጠርዝ የሚገኝ ከፍታ ያለው መሬት ማለት ነው::

Genesis 41:4

የከፉና የከሱ

“ደካማና የከሱ” በዘፍጥረት 41:3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

መልካምና የወፈሩ

“ጤናማና የደለቡ ወይም በደንብ የበሉ” በዘፍጥረት 41:2 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ነቃ

ከእንቅልፉ ነቃ

ሁለተኛ ጊዜ

“ሁለት” የሚለው ቃል ተራ ቁጥር ሁለት ነው:: አት “እንደገና” (ተራ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

እነሆ ዛላዎች

እዚህ እነሆ የሚለው ቃል ፈርዖን ባየው ነገር እንደተገረመ የሚያሳይ ነው

የእሸት ዛላዎች

ዛላዎች ፍሬዎች የሚንዠረግጉበት የበቆሎ ተክል አካል ነው

በአንድ የእህል አገዳ ላይ

“በአንድ አገዳ ላይ ያፌራውን ወይም የተንዠረገገውን” አገዳ ወፍራምና ረጅም የተክል ክፍል ነው::

በአንዱ አገዳ ላይ የተንዠረገገና ያማረ

በአንድ አገዳ ጤናማና ያማረ

የቀጨጩና በምሥራቅ ንፋስ የተመቱ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ያም ከምሥራቅ ደረቅ አየር የትነሳ የቀጨጩና በዋግ የተመቱ” (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የምሥራቅ ንፋስ

የምሥራቅ ንፋስ ከረሃማ ተነሥቶ የሚነፍስ ነው፡፡ የምስራቅ ንፋስ ሙቀት እጅግ ጐጂ ነው፡፡

ዛላዎች ወጡ

ዛላዎች አደጉ ወይም ተንዠረገጉ

Genesis 41:7

የቀጨጩ የእሸት ወይም የእህል ዛላዎች

እህል የተባለው ቃል የታወቀ ነው:: አት “የቀጨጩ የእህል ዛላዎች” (የተደበቁ ቃላትን የመግልጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ዋጡአቸው

በሉአቸው ሰው ምግብን እንደሚበላ የቀጨጩ የእሸት ዛላዎች ጤናማ የእሸት ዛላዎች ሲውጡ ፈርዖን በሕልሙ አየ

ሙሉና ፍሬያቸው የተንዠረገገውን የእሸት ዛላዎች

ጤናማና መልካም የእሸት ዛላዎች

በዘፍጥረት 41:5 የዚህ ተመሣሣይ ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ ነቃ

ከእንቅልፉ ነቃ

እነሆ

እዚህ እነሆ የሚለው ቃል ፈርዖ ባየው ነገር እንደተገረመ ያሳያል

ሕልም ነበር

ሕልም ሲያልም ነበር

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ የተጠቀመው የታሪኩ አድስ ክፍል መጀመሩን ለማመልከት ነው:: በቋንቋዎ ይህን የሚገልጹበት መንገድ ካለ ይጠቀሙ:: (አድስ ክስተት ስለማስታወቅ ይጠቀሙ)

መንፈሱ ታወከበት

እዚህ መንፈሱ የሚለው ቃለ የውስጥ ማንነቱን ወይም ስሜቱን ያመለክታል አት “በውስጥ ማንነቱ ታወከ” ወይም “ታወከ” (ተመሣሣይ ምትክ ቃል ስለመጠቀም ይመልከቱ)

ልኮና አስጠርቶ

አገልጋዮቹን እንደላካቸው መረዳት ይቻላል:: አት “እንዲጠሩ አገልጋዮቹን ላካቸው ወይም አገልጋዮቹ እንደጠሩ አዘዛቸው” (የተደበቁ ቃላትን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

የግብጽ አስማተኞችንና ጥበበኞች

የጥንት ነገሥታት አስማተኞችንና ጥበበኞችን እንደአማካሪዎች ይጠቀሙ ነበር

Genesis 41:9

የመጠጥ አሳላፊዎችን አለቃ

ይህ ለንጉሡ መጠጥን የሚያዘጋጅና የሚያቀርብ መሪ ሰው ነበር፡፡ በዘፍጥረት 4ዐ፡2 እነዚህ ቃላት እንዴት እንደተተረጐሙ ይመልከቱ፡

የሠራሁት በደል ዛሬ ታወሰኝ

ዛሬ የሚለው ቃል የተጠቀመው አስንዎት ለመስጠት ነው በደሉ ቀደም ብሎ ለፈርዖን መናገር የነበረበት አንድ ነገር ነገር ግን ያልተናገረበት ነው:: አት “ለአንተ መናገር የረሳሁትን አሁን አስታወስኩ”

ፈረዖን ተቆጥቶ ነበር

የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ፈርዖንን አንደ ሶሰተኛ ወገን ሰው ያመለክታል ይህም አነስተኛ ኃላፊነት ያለው ከፍተኛ ኃላፊነት ያለው የሚያስቀምጥበት የተለመደ መንገድ ነው እርስዎ ፈርዖን ተቆጥተው ነበር (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ከእርሱ አገልጋዮች ጋር

እዚህ እርሱ ፈርዖንን ያመለክታል አገልጋዮች የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃና የእንጀራ ቤት አዛዥ ያመለክታል:: አት “እኛ አገልጋዮችህ” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

እኔንና የእንጀራ ቤት አዛዡን በዘበኞች አለቃ ግቢ አስሮን ነበር

እኔንና የእንጀራ ቤት አዛዡን በዘበኞች አለቃ ኃላፊነት በተሰጠው እስር ቤት እስሮን ነበር:: እዚህ “ቤት” እስር ቤትን ያመለክታል::

የዘበኞች አለቃ

ንጉሡ ጠባቂዎች ላይ ኃላፊነት የተሰጠው ወታደር ነው በዘፍጥረት 2ዐ:2-3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

የእንጀራ ቤት አዛዥ

ለንጉሡ ምንብን የሚያዘጋጅ ዋና አስፈላጊ ሰው ነው፡፡ በዘፍጥረት 2ዐ:2-3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

እርሱና እኔ በአንዲት ሌሊት ሕልም አየን

“እኛ ሁለታችን በአንድ ሌሊት ሕልም አለምን” እዚህ እኛ የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃንና እንጀራ ቤት አዛዡን ያመለክታል (ነጠላና ብዙ እኛ ይመልከቱ)

የእያንዳንዳችን ሕልም የራሱ የሆነ ትርጉም ነበረው

ሕልሞቻችን የተለያየ ትርጉም ነበራቸው

Genesis 41:12

አጠቃላይ መረጃ

የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ለፈርዖ መናገሩን ቀጠለ

ከእኛ ጋር ነበር

በእስር ቤት ከእንጀራ ቤት አዛዥና ከእኔ ጋር ነበር

የዘበኞች አለቃ

ንጉሡ ጠባቂዎች ላይ ኃላፊነት የተሰጠው ወታደር ነው በዘፍጥረት 2ዐ:2-3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ሕልሞቻችንን በነገርነው ጊዜ ፊቺውን ነገረን

ሕልሞቻችንን ነገርነው እናም እርሱ ትርጉምቻቸውን ነገረን

ለእያንዳንዳችን እንደሕልማችን ተረጐመልን

እዚህ እርሱ ወይም እያንዳንዱ የሕልሙ ተርጓሚውን ሳይሆን የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃንና የእንጀራ ቤት አዛዥ በግል የሚያመለክት ነው አት ለእያንዳንዳችን ምን ሊሆን እንዳለ አስረዳን (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አጠቃቀም ይመልከቱ)

በዚያን ጊዜ

ይህ ሀረግ የተጠቀመው በታሪኩ አስፈላጊ ክስተት ለማመልከት ነው በቋንቋዎ ይህን መግለጽ የሚችሉበት መንገድ ካለ ይጠቀሙ

እርሱ እንደተረጐመልን ሆነ

ስለሕልሞቻችን እንደነገረን ሆነ

ፈርዖን ወደ ሹሜቴ መለሰኝ

እዚህ የመጠጥ አሳላፊዎች አለቃ ማከበሩን ለመግለጽ የፈርዖን የማዕረግ ስም ይጠቀማል:: አት ወደ ሥራዬ እንዲመለስ ፈቀድክልኝ (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

እርሱን ወይም ሌላኛውን

የእንጀራ ቤት አዛዡን

እርሱ ሰቀለው

እዚህ እርሱ ፈርዖንን ያመለክታል እና ይህም የእንጀራ ቤት አዛዡን እንዲሰቅሉት ፈርዖን ወታደሮቹን ማዘዙን ይወክላል አት እንዲሰቀል እርስዎ ወታደረችዎን አዝዘዋል:: (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽና ተዛማጅ ምትክ ቃላትን ስለመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ

Genesis 41:14

ፈርዖንም ሊኮ አስጠራ

ፈርዖን አገልጋዮቹን እንደላከ ይታወቃል አት ዮሴፍን እንዲያመጡት አገልጋዮችን ላከ (የተደበቁ ቃሎችን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ከግዞት ቤት

“ከእስር ቤት” ወይም “ከወህኒ”

ጸጉሩን ከተላጨ

በፈርዖን ፊት ለመቅረብ በመዘጋጀት ጊዜ የፊትና የራስ ጸጉርን መላጨት የተለመደ ተግባር ነበር

ፈርዖን ፊት መጣ

እዚህ መጣ የሚለው ገባ በሚለው ሊገለጽ ይችላል አት ፈርዖን ፊት ገባ (መጣ እና ገባ ይመልከቱ)

የሚተረጉመውም አልተገኘም

ሊተረጉምልኝ የቻለ አንድም ሰው አልተገኘም

አንተ የመተርጐም ችሎታ አለህ

አንተ ትርጉሙን ሊትነግረኝ ትችላለህ

ይህ በእኔ አይደለም

እኔ የመተርጐም ችሎታ የለኝም

እግዚአብሔር በደኀንነት ለፈርዖን ይመልስለታል

እግዚአብሔር ለፈርዖን የሚሻውን ትርጉም ይሰጠዋል

Genesis 41:17

እነሆ ቆሜ ነበር

ስለሚያስገርመው መረጃ ዮሴፍ ትኩረት እንዲሰጠው ፈርዖን “እነሆ” የሚለውን ቃል ይጠቀማል

በዐባይ ወንዝ ዳር

በዐባይ ወንዝ ዳርቻ የለውን ከፍታ የለውን መሬት ያመለክታል:: በዘፍጥረት 41:3 የዚህ ተመሣሣይ ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት “በዐባይ ወንዝ ዳር”

እነሆ ሰባት ላሞች

ስለሚያስገርመው መረጃ ዮሴፍ ትኩረት እንዲሰጠው ፈርዖን “እነሆ” የሚለውን ቃል ይጠቀማል

የወፈሩና ያማሩ

“የተቀለቡ/የደለቡና ጤናማ” በዘፍጥረት 41:2 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

በቀጠማዎች ውስጥ ወይም በመስኩ ይሰማሩ ነበር

በወንዙም ዳር ያለውን ሣር ይመገቡ ነበር:: በዘፍጥረት 41:2 የዚህ ተመሣሣይ ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

Genesis 41:19

እነሆ ሰባት ሌሎች ላሞች

ስለሚያስገርመው መረጃ ዮሴፍ ትኩረት እንዲሰጠው ፈርዖን “እነሆ” የሚለውን ቃል ይጠቀማል

የከፉና የከሱ

አቅሜ ደካሞችና የከሱ ወይም የቀጨጩ በዘፍጥረት 41:3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

እንደዚህ የሚያስከፉ

“አስከፊ” የሚለው ረቂቅ ስም እንደ ቅጽል ሊተረጐም ይችላል:: አት “የሚያስከፉ ላሞች” ወይም “የማይጠቅሙ የሚመስሉ ላሞች” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

የወፈሩ ላሞች

“የደለቡ ወይም የተቀለቡ ላሞች” በዘፍጥረት 41:2 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

እንደዋጧቸው ምንም ሊታወቅ አይችልም ነበር

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “የከሱ ላሞች የወፈሩትን መዋጣቸውን ማንም ሊነግረው እስከማይችል ነበር:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 41:22

አጠቃላይ መረጃ

ፈርዖን ሕልሙን ለዮሴፍ መናገሩን ቀጠለ

በሕልሜ አየሁ

ይህ ፈርዖን ከነቃና ተመልሶ ከተኛ በኋላ ያየውን ሕልም ይጀምራል፡፡ አት “እንደገናም ሕልም አለምሁ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

እነሆ ሰባት የእሸት ዛላዎች

ስለሚያስገርመው መረጃ ዮሴፍ ትኩረት እንዲሰጠው ፈርዖን “እነሆ” የሚለውን ቃል ይጠቀማል::

ሰባት የእሸት ዛላዎች

የእሸት ወይም የእህል የሚለው አባባል የታወቀ ነው:: አት “ሰባት የእህል ዛላዎች” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

በአንድ አገዳ ሲወጡ

“በአንድ አገዳ ሲንዠረግጉ” አገዳ ወፍራምና ረጅም የተክል አካል ነው:: በዘፍጥረት 41:5 ይህን ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

እነሆ ሰባት ሌሎች የእሸት ዛላዎች

ስለሚያስገርመው መረጃ ዮሴፍ ትኩረት እንዲሰጠው ፈርዖን “እነሆ” የሚለውን ቃል ይጠቀማል::

የጠወለጉ

የደረቁና ፍሬ አልባ የሆኑ

በምሥራቅ ነፋስ

“ከበረሃማ ቦታ የሚነፍሰው የምሥራቅ ንፋስ” የምሥራቁ ንፋስ ሙቄት አብዛኛውን ጊዜ ለእህሎች እጅግ አደገኛ ነበር::

ተንዠረገገ

አደገ ወይም ፍሬ ሰጠ

የቀጨጩ የእሸት ወይም የእህል ዛላዎች

የእህል የሚለው ቃል የታወቀ ነው በዘፍጥረት 41:7 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ አት የቀጨጩ የእህል ዛላዎች (የተደበቁ ቃላትን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ዋጧቸው

“በሉ” ፈርዖን ያለመው ሕልም ሰው ምግብን እንደሚበላ ጤናማ ያልሆኑ የበቆሎ እህሎች ጤናማ ያልሆኑትን እንደበሉ ነው:: በዘፍጥረት 41:7 የዚህ ተመሣሣይ ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

የሚችል ማንም አልተገኘም

የሚችል አንድም አልተገኘም ወይም ማንም አልቻለም

Genesis 41:25

የፈርዖን ሕልሞች ተመሣሣይ ናቸው

ትርጉሞችም ተመሣሣይ ናቸው የሚል አንድምታ አለው:: አት “ሁለቱም ሕልሞች ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ሊያደርግ ያለውን ለፈርዖን አስታወቀው

ዮሴፍ ፈርዖንን እንደሳስተኛ ወገን ሰው ያናግረዋል ይህ አክብሮትን መግለጫ መንገድ ነው:: እንደ ሁለተኛ ወገን ሰው መግለጽ ይቻላል:: አት “ቶሎ ሊያደርግ ያለውን እያሳየህ ነው” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 41:27

አጠቃላይ መረጃ

ዮሴፍ የፈርዖንን ሕልም መተርጐም ይቀጥላል፡፡

የከሱና አስከፊ መልክ ያላቸው ላሞች

የቀጨጩና ዐቅሜ ደካማ ላሞች በዘፍጥረት 41:3 የዚህ ተመሳሳይ ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

በምሥራቅ ነፋስ የተመቱ ሰባት የቀጨጩ የእሸት ዛላዎች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ከምሥራቁ ሙቀት አዘል ነፋስ የተነሣ የቀጨጩ ሰባት የእህል ዛላዎች” (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ይህን ለፈርዖን የተናገርኩትን … ለፈርዖን ገልጦለታል

ዮሴፍ ፈርዖንን እንደ ሶስተኛ ወገን ሰው ያናግረዋል ይህም አክብሮች መግለጫ መንገድ ነው:: በሁለተኛ ወገን ሰው መልክ ልገለጽ ይችላል:: “እንደተናገርኩህ እነዚህ ይደረጋሉ…… ፈርዖን ለአንተ ገልጦልሃል” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

እይ ሰባት

“እኔ የሚናገረው እውነትና ጠቃሚ ነውና ትኩረት ስጥ፤ ሰባት”

በመላው የግብጸ ምድር እጅግ የተትረፈረፈ ጥጋብ የሚሆንባቸው ሰባት ዓመታት ይመጣሉ

ጊዜ እንደሚመጣና በወቅቱ በአንድ ቦታ እንደሚሆን ይህ ስለጥጋብ ዓመታት ይናገራል:: አት “የተትረፈረፈ ምግብ በግብጽ በመላው የግብጽ ምድር የሚሆንበት ሰባት ዓመታት ይመጣሉ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 41:30

አጠቃላይ መረጃ

ዮሴፍ የፈርዖንን ሕልምች መተርጐም ቀጠለ

ከዚህ በኃላ ሰባት የራብ ዓመታት ይሆናሉ

ወደ አንድ ቦታው ተንቀሳቅሶ እንደሚመጣ ነገር ተደርጐ ስለ ሰባት ዓመታት ራስ ተነግሮአል አት ከዚም በኋላ እጅግ ጥቂት ምግብ የሚሆንበት ሰባት ዓመታት ይሆናሉ (ዘይቤይዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የራቡ ዘመን አገሪቱን እጅግ ስለሚጐዳት … የጥጋቡ ዘመን ሁለ ጨርሶ አይታወስም::

….የሚመጣው የራብ ዘመን እጅግ ጽኑ ከመሆኑ የተነሣ የጥጋብ ዘመን ፈጽም ይረሳል:: ዮሴፍ ለጉዳዩ አጽንዖት ለመስጠት አንድን ሀሳብ በሁለት መንገድ ይገልጻል (ተመሣሣይ ተጓዳኝ አባባሎችን ይመልከቱ)

በግብጽ ምድር የጥጋብ ዘመን ሁሉ ይረሳል

ምድር ሰዎችን ያመለክታል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “የግብጽ ሰዎች የተትረፈረፈ ምግብ የነበረበትን ዓመታት ሁሉ ይረሳሉ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤና ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አገሪቱን ይጐዳሉ

አገር የሚለው የአገሪቷን መሬት ሰዎችና መላውን የአገሪቷን አካል ያመለክታል (ምትክ ቃላትን የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ከሚመጣው ራብ የተነሣ

ይህ ተከትሎ እንደሚመጣ እንደ አንድ ነገር ስለሚመጣው ራብ ወይም ድርቅ ይናገራል፡፡ አት “ከዚያ በኋላ በሚሆነው ራብ ወይም ድርቅ የተነሣ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሕልሙ ለፈርዖን በሁለት መልክ በድጋሚ መታየቱ ነገሩ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቈረጠ ስለሆነ ነው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እግዚአብሔር ሁለት ሕልሞችን የሰጠህ ነገሮች በእርግጥ እንደሚከሰቱ ለማሣየት ነው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 41:33

አጠቃላይ መረጃ

ዮሴፍ ለፈርዖን መናገሩን ቀጠለ

አሁንም

ይህ በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም ነገር ግን ስለሚቀጥለው ጠቃሚ ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ነው

እንግዲህ ፈርዖን … ይፈልግ

ዮሴፍ ለፈርዖን እንደ ሶስተኛ ወገን ሰው ይናገራል ይህ አክብሮትን የመግለጫ መንገድ ነው በሁለተኛ ወገን ሰው መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “አንተ ፈርዖን ፈልግ” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

በግብጽ ምድር ላይም ይሹመው

ይሹመው ማለት ኃላፊነት ይስጠው ማለት ነው፡፡ አት “በግብጽ ግዛት ላይ ኃላፊነት ይስጠው ወይም በግብጽ ግዛት ላይ ይሹመው (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የግብጽ ምድር

እዚህ ምድር በግብጽ ምድር ያሉ ሰዎችንና ሁሉን ነገር ይወክላል (ተመሣሣይ ተዛማጅ ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤ ይመልቱ)

በግብጽ ምድር ከሚገኘው የእህል ምርት አንድ አምሰተአኛውን ይውሰዱ

አምስተኛ የሚለው ቃል ክፍልፋይ ነው:: የግብጽን ምድር እህል ምርት በአምስት መደብ ይክፈሉ፤ ከዚያም አንዱን እጅ ወይም መደብ ይውሰዱ (ክፍልፋዮችን ይመልከቱ)

በሰባት የጥጋብ ዓመታት

የተትረፈረፈ ምግብ ባለባቸው ሰባት ዓመታት

Genesis 41:35

አጠቃላይ መረጃ

ፈርዖንን መምከሩን ቀጠለ

እነርሱም ይሰብስቡ

ሹማምንት ወይም ኃላፊዎች እንዲሰበስቡ ይደረግ

በእነዚህ በሚመጡት ጥጋብ ዓመታት

እነዚህ ዓመታት አንድ ነገር ተጉዞ ወደ አንድ ቦታ እንደማመጣ እንደሚመጡ ይናገራል:: አት “ቶሎ ሊመጡ ያሉ የጥጋብ ዓመታት” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በፈርዖን ሥልጣን ሥር ያከማቹ

በፈርዖን ሥልጣን ሥር የሚለው ሀረግ ፈርዖን ሥልጣን ይስጣቸው ማለት ነው አት እህሉን ለመሰብሰብ የፈርዖንን ሥልጣን ይጠቀም ፈሊጣዊ አነገጋር ይመልከቱ

እነርሱም ይህን ይጠብቁ

እነርሱ የሚለው ቃል እህሉ እንዲጠበቅ የሚያዝዙ ሹማምንቶችንና ወታደሮች ያመለክታል አት ሹማምቶች እህሉ እንዲጠበቅ በዚያው ወታደሮችን ይመድቡ ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ

እህሉ ለምድሪቱ ምግብ ይሆናል

ምድሪቱ ሰዎችን ትወክላለች አት እህሉም ለሰዎች ምግብነት ይሆናል (ምትክ ቃላት ስለመጠቀም ይመልከቱ)

በዚህ ሁኔታ ምድሪቱ በራብ አትጠፋም

እዚህ “ምድር” ሰዎችን ይወክላል:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት “በዚህ መንገድ በራብ ጊዜ ሰዎች አይራቡም” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤ ወይም ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 41:37

ይህ ምክር ለፈርዖንና በሎለዎቹ ፊት መልካም ሆነ

ፊት ማየትን የሚያመለክት ሲሆን ማየት ማሰብን ወይም ብያኔን ያመለክታል አት ፈርዖንና ሎሌዎቹ ይህ መልካም እቅድ ሆኖ አገኙት

ሎሌዎች

የፈርዖ ሹማምንት

እንደዚህ ያለ ሰው

ዮሴፍ የገለጸው ዓይነት ሰው

የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት

የእግዚአብሔር መንፈስ የሚኖርበት

Genesis 41:39

እንዳንተ ያለ ብልህ የለም

እንዳንተ ያለ ውሳኔ አቅራቢ የለም:: በዘፍጥረት 41:33 ብልህ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

አንተ የቤተመንግሥቴ የበላይ ትሆናለህ

እዚህ “ቤት” የፈርዖን ቤተመንግሥትና በቤተመንግሥቱ ያሉ ሰዎችን ይወክላል:: የበላይ የሚለው ሀረግ ዮሴፍ የበላይ ኃላፊነት ይሰጠዋል ማለት ነው:: አት በቤተመንግሥቴ በሁሉም ላይ ሥልጣን ይሰጥሃል:: (ምትክ ቃላት ስለመጠቀም ዘይቤና ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሕዝቤ ሁሉ ለሥልጣኔ ይገዛል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል በሕዝቤ ላይ ገዥ ትሆናለህና አንተ የሚታዝዘውን ያደርጋሉ:: (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በዙፋኔ ብቻ

እዚህ ዙፋን ፈርዖን እንደንጉሥ ገዥ እንደሆነ ይገልጻል:: አት “በንጉሥነት ሚናዬ ብቻ”

እየው አድርጌሃለሁ

“እየው” የሚለው ቃል ፈርዖን በሚቀጥለው ለሚናገረው አጽንዖት ይሰጣል:: አት “እየው አድርጌሃለሁ”

በመላይቱ የግብጽ ምድር ላይ ኃላፊ አድርጌሃለሁ

የበላይ አድርጌሃለሁ ማለት ሥልጣን ሰጥቼሃለሁ ማለት ነው እዚህ ምድር ሰዎችን ያመለክታል አት በግብጽ ምድር ባለው በማንኛውም ላይ ኃላፊነት ሰጥቼሃለሁ (ምትክ ቃል የመጠቀም ዘይቤና ፈሊጣዊ አነጋገር ይጠቀሙ)

Genesis 41:42

ፈርዖንም ባለማኀተሙን ቀለበት አውልቆ …. የወርቅ ሐብል አጠለቀለት

እነዚህ ሁሉ ድርጊቶች የሚያመለክቱት ዮሴፍ ያቀደውን ሁሉ እንዲያደርግ ፈርዖን ለዮሴፍ ሥልጣን መስጠቱን ነው (ምልክታዊ ድርጊት የመልከቱ)

ባለማኀተሙ ቀለበት

ይህ ቀለበት የፈርዖን ማኀተም የተቀረጸበት ነው:: ይህም ያቀደውን እንዲያከናውን ለዮሴፍ ገንዘብና ሥልጣንን ሰጠው::

ከጥሩ የተልባ እግር የተሠራ ልብስ

የተልባ እግር የተሠራ ልብስ ሰማያዊ አበባ ካለው የተልባ እግር የተሠራ ለስላሳ ጠንካራ ልብስ ነው::

የእርሱም በሆነው ሁለተኛው ሠረገላ ላይ አስቀመጠው

ይህ ድርጊት ለሰዎች ግልጽ የሚያደርገው የፈርዖን ሁለተኛ ሰው ዮሴፍ ብቻ መሆኑን ነው (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

ስገዱ ወይም እጅ ንሡ

ስገዱና ዮሴፍን አክብሩ እጅ መንሣትና መስገድ ክብርንና አክብሮትን የመስጠት ምልክት ነው (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

ፈርዖን በምድሪቱ ባለው ማንኛውም ላይ ሾመው

ማንኛውም ላይ ሾመው የሚለው ሀረግ ሁሉ ላይ ስልጣን ሰጠው ማለት ነው:: እዚህ ምድር ሰዎችን ያመለክታል በዘፍጥረት 41:41 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት “በግብጽ ባለው ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጠሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገርና ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 41:44

እኔ ፈርዖን ነኝ … ያለ አንተ

ፈርዖን የራሱን ሥልጣን አጽንቶ ይናገራል፡፡ አት “እንደ ፈርዖን እኔ የማዝዘው ያለአንተ”

ያላንተ ማንም እጁንም እግሩንም አያንሣ

እዚህ “እጅና እግር” የሰዎችን ድርጊቶች ይወክላሉ:: አት “ማንኛውም ሰው ምንም ነገር ያለፈቃድህ በግብጽ አያድርግ ወይም ማንኛውም ሰው ምንም ነገር በግብጽ ከማድረጉ በፊት ያንተን ፈቃድ ይጠይቅ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ማንም ሰው

እዚህ “ሰው” ወንድም ሆነ ሴት በአጠቃላይ ማንንም ሰው ያመለክታል:: (በወንድ ጾታ የተገለጹ ቃላት ለሴት ጾታም መሆናቸውን ይመልከቱ)

ጸፍናት ፐዕናህ

ተርጓሚዎች የሚከተውን በግርጌ ማስታወሻ ሊጠቀሱ ይችላሉ:: “ጸፍናት ፐዕናህ” የሚለው ስም “ሚስጢሮችን ገላጭ” ማለት ነው፡፡

የሄልዮቱ ወይም ዖን ከተማ ካህን የጶጥፌራ ልጅ የሚትሆን አስናትን አጋባው

ጶጥፋራ የአስናት አባት ነው:: “ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ”

የሄልዮቱ ካህን

ዖን የጸሐይ አምላክ ራአ አምልዕኮ ማዕከል ያለባትና “የጸሐይ ከተማ” የነበረች እንዲሁም “ሄልዮቱ” ተብላ የሚትጠራ ከተማ ነች (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዮሴፍም በመላይቱ የግብጽ ምድር ተዘዋወረ

ሊመጣ ስላለው ያልታሰበ የድርቅ ጊዜ ዝግጅት ለማድረግ ዮሴፍ በመላይቱ የግሣብ ምድር ተዘዋወረ

Genesis 41:46

ሠላሳ ዓመት ዕድሜ

3ዐ ዓመት ዕድሜ ቁጥሮችን ይመልከቱ

ዮሴፍም በፈርዖን ፊት በቆመ ጊዜ

እዚህ በፊቱ መቆም ዮሴፍ ፈርዖንን ማገልገል መጀመሩን ያሳያል:: አት “ፈርዖንን ማገልገል በጀመረ ጊዜ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

በመላይቱ የግብጽ ምድር ተዘዋወረ

ዮሴፍ ዕቅዱን ለማከናወን ዝግጅት ሲያደርግ አገሪቱን በጥንቃቄ እንደመረመረ ነው

በሰባቱም የጥጋብ ዓመታት

በሰባቱም መልካም ዓመታት

ምድሪቱ የተትረፈረፈ ሰብል ሰጠች

ምድራቱ ብዙ እህል አመረተች

Genesis 41:48

እርሱም ምርት ሰብስቦ …. አከማቸ

እዚህ “እርሱ” የዮሴፍን አገልጋዮች ያመለክታል:: አት “ዮሴፍ አገልጋዮቹ እንዲሰበስቡ አዘዘ …. አከማቹ (ከፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ዮሴፍ እንደ ባሕር አሸዋ እጅግ ብዙ እህል አከማቸ

የእህሉን እጅግ መብዛት በአጽንዖት ለመናገር ከባሕር አሸዋ ጋር ያነጻጽራል፡፡ አት “ዮሴፍ ያከማቸው እህል ባህር ዳር እንዳለ አሸዋ እጅግ ብዙ ነበር” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ዮሴፍ አከማቸ …. እርሱም አቆመ

እዚህ ዮሴፍ እና እርሱ የዮሴፍን አገልጋዮች ይወክላል:: አት “ዮሴፍ አገልጋዮቹ እንዲያከማቹ አደረገ … እነርሱም አቆሙ” (ከፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 41:50

የራብ ዓመታት ከመምጣታቸው በፊት

ሰባቱ የራብ ዓመታት ከመምጣቱ በፊት ይህም አንድ ነገር ተጉዞ ወደ አንድ ቦታ እንደሚመጣ ተደርጐ ስለሚመጡ ዓመታት ይናገራል:: አት “ሰባቱ የራብ ዓመታት ከመጀመራቸው በፊት” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አስናት

የአንዲት ሴት ስም ነው:: በዘፍጥረት 41:45 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የዖን ካህን

ዖን የጸሐይ አምላክ ራአ አምልዕኮ ማዕከል ያለባትና “የጸሐይ ከተማ” የሆነች እንዲሁም “ሄልዮቱ” ተብላ የሚትጠራ ከተማ ነች፡፡ በዘፍጥረት 41:45 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ምናሴ

ተርጓሚዎች የሚከተለውን በግርጌ ማስታወሻ ሊጠቀሙ ይችላሉ:: “ሚናሴ” የሚለው ስም ለመርሳት ምክንያት መሆን ማለት ነው::

የአባቴንም ቤት

ይህ የዮሴፍ አባት ያዕቆብንና ቤተሰቡን ያመለክታል

ኤፍሬም

ተርጓሚዎች የሚከተለውን የግርጌ ማስታወሻ ሊጨምሩ ይችላሉ:: “ኤፍሬም” የሚለው ስም “ፍሬያማ መሆን” ወይም “ልጆችን መውለድ” ማለት ነው::

ፍሬያማ አደረገኝ

“ፍሬያማ” መበልጸግ ወይም ልጆችን መውለድ ማለት ነው:: (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በተሠቃየሁበት ምድር

“ሥቃይ” የሚለው ረቂቅ ስም “መከራ ተከበልኩ” በሚለው ሊገለጽ ይችላል:: አት “መከራን በተቀበልሁት ምድር” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

Genesis 41:53

በየአገሩ ሁሉ

ከግብጽ ባለፈ የከነዓንንም ምድር ጨምሮ በዙሪያው ባሉ አገሮች ሁሉ

በመላው የግብጽ ምድር ግን ምግብ ነበር

ይህም የሚያስረዳው በሰባት መልካም ዓመታት ሕዝቡ እህልን እንዲያጠራቅሙ ዮሴፍ ስላዘዛቸው ምግብ ነበራቸው (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 41:55

ራብ በመላው የግብጽ ምድር መስፋፋት ሲጀምር

እዚህ “ምድር” ሰዎችን ይወክላል:: አት “ግብጻዊያን ሁሉ በተራቡ ጊዜ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ራቡ በአገሩ ሁሉ ፊት እየተስፋፋ ስለሄደ

እዚህ ፊት የሚለው ቃል ምድር ላይ ማለትን ያመለክታል:: አት “ራቡ በየአገሩ ተስፋፋ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ዮሴፍ ጐተራዎችን ሁሉ ከፍቶ እህሉ ለግብጻዊያን እንዲሸጥ አደረገ

እዚህ “ዮሴፍ” የዮሴፍን አገልጋዮች ይወክላል:: አት “ዮሴፍ አገልጋዮቹ ጐተራዎችን ሁሉ እንዲከፍቱና ለግብጻዊያን እህል እንዲሸጥ አደረገ” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ከምድር ሁሉ ወደ ግብጽ ይመጡ ነበር

እዚህ ምድር ከሁሉ አገራት የሆኑ ሰዎችን ይወክላል:: አት “በዙሪያው ካሉ አገሮች ሁሉ ሰዎች ወደ ግብጽ ይመጡ ነበር” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

በምድር ሁሉ

በመላው ምድር በግብጻዊያንን የንግድ መሥመሮች የሚጠቀሙ በድርቅ የተጠቁ የተለያዩ የንግድ አጋሮችና አገሮች ሁሉ ወደ ግብጽ ይመጡ ነበር እንደማለት ነው


Chapter 42

1 በግብፅ እህል መኖሩን ሲሰማ፣ ልጆቹን እንዲህ አላቸው፤ “ለምን እርስ በርስ ትተያያላችሁ?” 2 በግብፅ አገር እህል መኖሩን ሰምቻለሁ፤ በራብ ከመሞታችን በፊት ወደዚያ ሂድና እህል ግዙልን” አላቸው። 3 ስለዚህ ዐሥሩ የዮሴፍ ወንድሞች እህል ለመግዛት ወደ ግብፅ ሄዱ። 4 ነገር ግን ያዕቆብ የዮሴፍን ወንድም ብንያምን ክፉ ነገር ይደርስበታል በሚል ፍርሃት ከወንድሞቹ ጋር አልላከውም። 5 ራቡ በከነዓንም በመበርታቱ፣ እህል ለመሸመት ወደ ግብፅ ከሄዱት መካከል የእስራኤል ልጆችም ነበሩ። 6 በዚህ ጊዜ ዮሴፍ የምድሪቱ ገዢ ነበር፣ ለአገሩ ሰዎች ሁሉ እህል የሚሸጥላቸው እርሱ ነበር። የዮሴፍ ወንድሞችም እንደደረሱ ከፊቱ ቀርበው ወደ ምድር ለጥ ብለው ሰገዱለት። 7 ዮሴፍም ወንድሞቹን ባየ ጊዜ ዐወቃቸው፣ ነገር ግን የማያውቃቸው በመምሰል በቁጣ ቃል፣ “ከየት ነው የመጣችሁት?” ብሎ ጠየቃቸው። እነርሱም፣ “እህል ለመሸመት ከከነዓን ምድር የመጣን ነን" ብለው መለሱለት። 8 ዮሴፍ ወንድሞቹን ቢያውቃቸውም እንኳ እነርሱ ግን አላወቁትም። 9 በዚህ ጊዜ ስለወንድሞቹ ያየው ሕልም ትዝ አለውና፣ “ሰላዮች ናችሁ፣ የመጣችሁት አገራችን በየትኛው በኩል ለጥቃት የተጋለጠች መሆኗን ለመሰለል ነው” አላቸው። 10 እነርሱም እንዲህ አሉት፤ “ጌታችን ሆይ፣ እንዲህስ አይደለም፤ እኛ አገልጋዮችህ የመጣነው እህል ለመሸመት ነው፤ 11 ሁላችንም የአንድ አባት ልጆች ነን፤ አገልጋዮችህም የታመንን ሰዎች እንጂ ሰላዮች አይደለንም።” 12 እርሱም መልሶ፣ “አይደለም፣ ግብፅ በየት በኩል ለጥቃት የተጋለጠች መሆኗን ለመሰለል ነው” አላቸው። 13 እነርሱ ግን መልሰው፣ “እኛ አገልጋዮችህ በከነዓን አገር ከሚኖር ከአንድ ሰው የተወለድን ዐሥራ ሁለት ወንድማማቾች ነን። ትንሹ ወንድማችን አባታችን ዘንድ ሲሆን አንዱ ወንድማችን ሞቷል። 14 ዮሴፍም እንዲህ አላቸው፤ “ነገርኋችሁ እኮ፤ ሰላዮች ናችሁ 15 ታናሽ ወንድማችሁ እዚህ እስካልመጣ ድረስ ከዚህ ንቅንቅ እንደማትሉ በፈርዖን ስም እምላልሁ፤ ማንነታችሁ የሚረጋገጠውም በዚህ ነው። 16 ከእናንተ አንዱ ሄዶ ወንድማችሁን ያምጣ፤ የተናገራችሁትም እውነት መሆኑ ተረጋግጦ ነጻ እስክትለቀቁ ድረስ የቀራችሁት እዚሁ በእስት ቤት ትቆያላችሁ፤” 17 ሁሉንም ሦስት ቀን በእስር አቆያቸው። 18 በሦስተኛውም ቀን ዮሴፍ እንዲህ አላቸው፤ “እኔ እግዚአብሔርን ስለምፈራ እንዲህ በማድረግ ሕይወታችሁን አትርፉ። 19 ታማኝ ሰዎች ከሆናችሁ፣ ከመካከላችሁ እንዱ እዚህ እስር ቤት ሲቆይ፣ የቀራችሁት ግን ለተራቡት ቤተ ሰቦቻችሁ እህል ትወስዱላቸዋላችሁ፤ 20 ታናሽ ወንድማችሁን ግን ይዛችሁ መምጣት አለባችሁ፤ በዚህም የተናገራችሁት ቃል እውነተኛነት ይረጋገጣል፤ እናንተም ከመሞት ትተርፋላችሁ።” እነርሱም ይህንኑ ለመፈጸም ተስማሙ። 21 እርስ በርሳቸውም እንዲህ ተባባሉ፤ “በእርግጥ በወንድማችን ላይ ስላደረስነው በደል ቅጣታችንን እየተቀበልን ነው። እርሱ እንደዚያ ተጨንቆ ስለ ሕይወቱ ሲማጠነን፣ እኛ አልሰማነውም ነበር፤ ይህ መከራ የደረሰብንም በዚሁ ምክንያት ነው” ተባባሉ። 22 ሮቤልም መልሶ፣ “በዚህ ልጅ ላይ ክፉ ነገር እንዳታደርጉ ብዬ አልነበረምን? እናንተ ግን አልሰማችሁኝም፤ ስለዚህም ደሙ ከእጃችን ይፈለጋል” አላቸው። 23 ዮሴፍ የሚያነጋግራቸው በአስተርጓሚ ስለሆነ የሚነጋገሩትን እንደሚሰማባቸው ዐላወቁም ነበር። 24 ከፊታቸውም ዘወር ብሎ አለቀሰ፤ ከዚያም ወደእነርሱ ትመልሶ እንደገና አነጋገራቸው፤ ስምዖንንም ከእነርሱ ለይቶ ዓይናቸው እያየ አሰረው፤ 25 ዮሴፍ ለአገልጋዮቹ በስልቻዎቻቸው እህል እንዲሞሉላቸው፤ ብሩንም በያንዳንዱ ሰው ስልቻ ውስጥ መልሰው እንዲያስቀምጡና ለጉዞአቸው ስንቅ እንዲያሲዟቸው ትእዛዝ ሰጠ። ይህም ተደረገላቸው። 26 እነርሱም እህላቸውን በአህዮቻቸው ጭነው ጉዞአቸውን ቀጠሉ። 27 በመንገድም ለአዳር ሰፍረው ሳለ፣ ከእነርሱ አንዱ ከያዘው እህል ላይ ለአህያው ለመስጠት ስልቻውን ሲፈታ፣ በስልቻው አፍ ላይ ብሩን አገኘ። 28 እርሱም ወንድሞቹን፣ “ኧረ ብሬ ተመልሶልኛል፤ ይኸው ስልቻዬ ውስጥ አገኘሁት” አላቸው። ሁሉም ልባቸው በድንጋጤ ተሞልቶ እየተንቀጠቀጡ በመተያየት፣ “እግዚአብሔር ምን ሊያመጣብን ይሆን?” አሉ። 29 በከነዓን ምድር ወዳለው ወደ አባታቸው ወደ ያዕቆብ ከደረሱ በኋላ ያጋጠማቸውን ሁሉ እንዲህ ብለው ነገሩት፤ 30 “የግብፅ አገር አስተዳዳሪ ‘አገሬን ልትሰልሉ የመጣችሁ ናችሁ’ በማለት በቁጣ ቃል ተናገረን፤ 31 እኛ ግን እንዲህ አልነው፤ “እኛ የታመንን ሰዎች እንጂ ሰላዮች አይደለንም። 32 እኛ የአንድ አባት ልጆች የሆንን ዐሥራ ሁለት ወንድማማቾች ነን፣ አንዱ የለም፣ ታናሽ ወንድማችን ግን ከአባታችን ጋር በከነዓን ይገኛል።’ 33 ከዚህ በኋላ የአገሩ ጌታ የሆነው ሰው እንዲህ አለን፣ “ታማኝ ሰዎች መሆናችሁን የማውቀው በዚህ ነው ከእናንተ መካከል አንዱን ወንድማችሁን እዚህ እኔ ዘንድ ትታችሁ የተቀራችሁት ለትራቡት ቤተ ሰቦቻችሁ እህል ይዛችሁላቸው ሂዱ። 34 ነገር ግን ታናሽ ወንድማችሁን ወደ እኔ አምጡት። በዚያን ጊዜም ታማኝ ሰዎች እንጂ ሰላዮች አለመሆናችሁን ዐውቃለሁ፤ ወንድማችሁንም መልሼ እሰጣችኋለሁ፤ እናንተም በምድሪቱ እንደፈለጋችሁ እየተዘዋወራችሁ መነገድ ትችላላችሁ። 35 እህሉንም ሲዘረግፉ በየስልቻቸው ውስጥ ብራቸው እንደተቋጠረ ተገኘ፤ የእያንዳንዳቸውን የተቋጠረ ብር ሲያዩም፣ እነርሱም ሆኑ አባታቸው ደነገጡ። 36 አባታቸው ያዕቆብም፣ “ያለ ልጅ እኮ አስቀራችሁኝ፣ ዮሴፍ የለም፣ ስምዖንም የለም፤ አሁን ደግሞ ብንያምን ልትወስዱ ትፈልጋላችሁ፤ በዚህ ሁሉ መከራ የምሠቃየው እኔ ነኝ” አለ። 37 በዚህን ጊዜ ሮቤል አባቱን፣ “ብንያምን ወደ አንተ መልሼ ባላመጣው ሁለቱን ወንዶች ልጆቼን ወስደህ ግደላቸው፣ ስለዚህ በእኔ ኃላፊነት ላከው፤ እኔም መልሼ አመጣዋለሁ” እለው። 38 ያዕቆብም “ምንም ቢሆን ከእናንተ ጋር አይሄድም፤ ወንድሙ ሞቶአል፣ የቀረው እርሱ ብቻ ነው፤ በመንገድ አንድ ጉዳት ቢደርስበት በእርጅናዬ ዘመን በመሪር ሐዘን ወደ መቃብር እንድወርድ ታደርጉኛላችሁ” አላቸው።



Genesis 42:1

አሁንም ያዕቆብ ….እንዲህ አላቸው

አሁንም የሚለው ቃል የታሪኩን አዲስ ክፍል ያመለክታል (አድስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

ለምን እርስበርስ ትተያያላችሁ?

ስለ እህል ምንም ባለማድረጋቸው ልጆቹን ለመቆጣት ያዕቆብ ጥያቄ ይጠቀማል:: አት “እዚሁ ዝም ብላችሁ አትቀመጡ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ወደዚያ ይውረዱ …. ወረዱ

ከከነዓን ወደ ግብጽ መሄድ ወደ ታች እንደመውረድ መናገር የተለመደ ነበር

ከግብጽ

እዚህ “ግብጽ” ሰዎች እህልን የሚሸጡበት ያመለክታል:: አት “በግብጽ እህልን ከሚሸጡ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

ያዕቆብ የዮሴፍን ወንድም ብንያምን … አልላከውም

ብንያምና ዮሴፍ አንድ አባትና እናት ነበራቸው የዕቆብ የራሔል መጨረሻ ልጅዋ እንዲጐዳ ወይም ክፉ ነገር እንዲደርስበት አልፈለገም ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይጠቀሙ

Genesis 42:5

የእስራኤል ልጆች ለእህል ሸመታ ከመጡበት ጋር

“መጡ” የሚለው ቃል “ሄዱ” በሚለው ሊተረጐም ይችላል:: እንዲሁም እህል እና ግብጽ የተባሉ ቃላት የታወቁ ናቸው:: አት “የእስራኤል ልጆች እህል ለመሸመት ከሌሎች ሰዎች ጋር ወደ ግብጽ ሄዱ” (ሄደ እና መጣ አጠቃቀምና ድብቅ ቃላት የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በዚህን ጊዜ ዮሴፍ

“በዚህን ጊዜ” ታሪኩ ወደ ዮሴፍ ሕይወት መረጃ መቀየሩን ያመለክታል:: (የዳራ መረጃ ይመልከቱ)

በምድሪቱ ላይ

ምድር ግብጽን ያመለክታል:: አት “በግብጽ ላይ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ለአገሩ ሰዎች ሁሉ

እዚህ አገር ግብጽንና ዙሪያው ያሉ አገሮችን ያጠቃልላል አት እህል ለመሸመት ከተለያዩ አገሮች ለመጡ ሰዎች ሁሉ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የዮሴፍም ወንድሞች መጡ

“መጡ” እንደ “ሄዱ” ሊተረጐም ይችላል:: (መጣ እና ሄደ አጠቃቀም ይመልከቱ)

በግምባራቸው ወደ ምድር ጐንበስ ብለው ሰገዱለት

ይህ አክብሮትን የመስጠት ምልክት ነው:: (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Genesis 42:7

ዮሴፍም ወንድሞቹን አይቶ አወቃቸው

ዮሴፍም ወንድዋቹን ባያቸው ጊዜ አወቃቸው

እንደማያውቃቸው ሆነ

“የእነርሱ ወንድም እንዳልሆነ ታየ” ወይም “ወንድማቸው እንደሆነ እንዲያውቁት አልፈለገም”

ከየት የመጣችሁ ናችሁ?

ዮሴፍ መልሱን ቢያውቅም ይህ አግናኝ ጥያቄ አልነበረም የራሱን ማንነት ለወንድሞቹ ላለመግለጽ የመረጠው መንገድ ነበር

Genesis 42:9

ሰላዮች ናችሁ

ሰላዮች ሌላ አገርን ለመጥቅ በስውር ስለአንድ አገር መረጃ ለማግኘት የሚጥሩ ሰዎች ናቸው::

ምድሪቱ በየትኛ በኩል የተጋለጠች እንደሆነች ሊታዩ መጥታችኋል

የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት አገራችን በየትኛው በኩል እንደተጋለጠች ለማየትና ከዚያም ሊታጠቁን ለማየት መጥታችኋል (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ጌታችን ሆይ

አንድን ሰው ለማክበር የሚጠቀሙበት አባባል ነው

ባሪያዎችህ

ወንድሞቹ ራሳቸውን እንደ ባሪያዎች አድርገው ያቀርባሉ፡፡ ይህም ከፍተኛ ሥልጣን ላለው ሰው የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው፡፡አት “እኛ ባሪያዎችህ” ወይም “እኛ” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 42:12

እርሱ ለእነርሱ አላቸው

ዮሴፍ ለወንድሞቹ አላቸው

አይደለም በየት በኩል ምድራችን ጥቃት የተጋለጠች መሆንዋን ለማየት ነው

የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “አይደለም በየት በኩል ምድራችን ለጥቃት የተጋለጠች መሆንዋን ለመሰለልና ከዚያም ሊታጠቁን ነው” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አሥራ ሁለቱ ወንድሞች

12ቱ ወንድሞች (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

እየው ትንሹ ወንድማችን

“ስማን ትንሹ ወንድማችን” “እየው” የሚለው ቃል ቀጥለው ለምነግሩት ነገር ትኩረት እንዲሰጥ ተጠቅሞአል::

ትንሹ ወንድማችን አባታችን ዘንድ ነው

“በዚህን ጊዜ ትንሹ ወንድማችን ከአባታችን ጋር ነው”

Genesis 42:14

ነገርኋች እኮ ሰላዮች ናችሁ

“እንደነገርኋችሁ ሰላዮች ናችሁ” (በዘፍጥረት 42;9 “ሰላዮች” እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ)

በዚህ ትፈተናላችሁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “የሚፈትናችሁ በዚህ ነው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በፈርዖን ሕይወት

ይህ ጠንከር ወይም ኮስተር ያለ መሃላ ነው አት በፈርዖን ሕይወት እምላለሁ

ከእናንተ አንዱን ላኩና ወንድማችሁን ይዞ ይመለስ

“ከእናንተ አንዱን ምረጡና ሂዶ ወንድማችሁን ይዞ ይመለስ”

እስር ቤት ትቆያላችሁ

የቀራችሁ በእሥር ቤት ትቆያላችሁ

የተናገራችሁት ቃል እውነት መሆኑ እስኪረጋገጥ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት እውነት መናገራችሁን እንዳውቅ (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልክቱ)

በግዞት ቤት

በእስር ቤት

Genesis 42:18

በሶስተኛውም ቀን

“ሶስት” የሚለው ተራ ቁጥር ነው:: አት “ከሁለተኛው ቀን በኋላ” (መቁጠሪያ ተራ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

እንዲህ በማድረግ ሕይወታችሁን አትርፉ

የተቀመጠው መረጃ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “የሚለውን ካደረጋችሁ በሕይወት ትተርፉ አደርጋችኋለሁ” (የተደበቁ ቃላትን ስለመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን እፈራለሁና

ይህ ከልብ እግዚአብሔርን ማክበርንና ያንን ለእርሱ በመታዘዝ መግለጽን ያመለክታል

አንዱ ወንድማችሁ በእሥር ቤት ይቆይ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ልገለጽ ይችላል:: አት “እንዱን ወንድማችሁን እዚሁ እሥር ቤት ተውት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እናንተ ግን ሂዱ

እዚህ ሂዱ ብዙ አመላካችና በእሥር ቤት የማይቆዩ ወንድሞች ሁሉን ያመለክታል (ብዙ አመላካች እናንተ ይመልከቱ)

ለተራቡት ቤተሰቦቻችሁ እህል ትወስዱላቸዋላችሁ

እዚህ ቤቶች ቤተሰቦችን ይወክላል:: አት “በዚህ ራብ ወቅት ቤተሰቦቻችሁን ለመርዳት እህል ትወስዱላቸዋላችሁ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

የተናገራችሁት ቃል እውነተኛነት ይረጋገጣል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት የሚትነግሩ እውነት መሆኑን አውቃለሁ (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ ይመልከቱ)

ከሞት ትተርፋላችሁ

ወንድሞቹ ሰላይ መሆናቸውን ካረጋገጠ ዮሴፍ በወታደሮቹ እንደሚያስገድላቸው የሚል ትርጉም ይኖረዋል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 42:21

ነፍሱ ስትጨነቅ አይተን

ነፍሱ ዮሴፍን ይወክላል አት ዮሴፍ እንደዚያ ሲጨነቅ አይተን ወይም ዮሴፍ እንደዚያ ሲሰቃይ አይተን (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ይህ ጭንቀት የደረሰብን በዚህ ምክንያት ነው

“ጭንቀት” የሚለው ረቂቅ ስም “መከራ” በሚለው ግሥ ሊተረጐም ይችላል:: አት “ይህ መከራ የደረሰብን በዚሁ ምክንያት ነው” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

በዚህ ልጅ ላይ ክፉ አታድርጉ ብዬ አልነበረምን? እናንተ ግን አልሰማችሁኝም

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ ይዞአል እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገልጽ ይችላል:: አት “በዚህ ልጅ ላይ ኃጢአት እንዳታደርጉ አልነገርኋችሁምን፤ነገር ግን” ወይም “ልጁ ላይ ክፉ እንዳታደርጉ ነግሬአችኋለሁ፤ ነገር ግን” (በጥቅሶች ውስጥ ጥቅሶችንና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

አሁንም እዩ

እዚህ አሁን በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም አሁን እና እዩ ሁለቱ የተጠቀሙት ለሚቀጥለው በጣም ጠቃሚ ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ነው

ደሙ ከእጃችን ይፈለጋል

እዚህ ደም የዮሴፍን ሞት ይወክላል ወንድምቹ ዮሴፍ እንደሞተ አስበዋል:: “ከእጃችን ይፈለጋል” የሚለው ሀረግ ስላደረጉት ነገር ይቀጣሉ ማለት ነው:: አት “ለሞቱ የሚገባውን ቅጣት እየተቀበልን ነን” ወይም “በመግደላችን መከራ እየተቀበልን ነን” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ወይም ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 42:23

በመካከላቸው አስተርጓሚ ነበረና …. አላወቁም

አስተርጓሚ አንድ ሰው የሚናገረውን ወደ ሌላ ቋንቋ የሚተረጉም ሰው ማለት ነው ዮሴፍ የእነርሱን ቋንቋ እንደማይናገር ለማስመሰል በራሱና በእነርሱ መካከል አስተርጓሚ አድርጐ ነበር

ከእነርሱ ዘወር ብሎ አለቀሰ

ዮሴፈ ወንድሞቹ የተናገሩትን በመስማቱ ስሜቱ ስለተነካ አለቀሰ (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ተናገራቸው

እስከዚህ ዮሴፍ ወንድሞቹን የሚያናግረው በተለየ ቋንቋ ስለሆነ አስተርጓሚ ይጠቀም ነበር (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ዐይናቸው እያየ አሠረው

እዚህ ለሚያዩት ነገር ትኩረት ለመስጠት ሰዎች በዐይኖች ተመስለዋል:: አት “በፊታቸው አሰረው” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

የመንገድ ስንቅ ይሰጡአቸው ዘንድ

ለጉዞአቸው ስንቅ እንዲሰጡአቸው

ይህም ተደረገላቸው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት ዮሴፍ ያዘዘውን ሁሉ አገልጋዮቹ አደረጉላቸው (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 42:26

ከእነርሱም አንዱ በአደረበት ሥፍራ ለአህያው ገፈራን ሊሰጥ ዘንድ ዓይበቱን ሲፈታ ብሩን አየ እነሆም በዓይበቱ አፍ ላይ ነበረች

በመንገድም አዳር ሰፍረው ሳሉ ከእነርሱ አንዱ ከያዘው እህል ላይ ለአህያው ለመስጠት ስልቻውን ሲፈታ በስልቻው አፍ ላይ ብሩን አየ

እነሆ

እዚህ እነሆ የሚለው ቃል ለሚቀጥለው አስገራሚ ሃሳብ ትኩረት እንድንሰጥ ለማድረግ ነው

ብሬ ተመልሶልኛል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልከ ሊገለጽ ይችላል አት አንድ ሰው ብሬን መልሳ አስቀመጠልኝ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልክቱ)

ይሄው ወደዚህ እዩ

ይሄው በስልቻዬ እዩ

ልባቸው በድንጋጤ ተሞላ

መፍራቻው ልባቸው በድንጋጤ እንደተዋጠ እንደተሞላ ተገልጾአል እዚህ ልብ በድፍረት ተመስሎአል አት እጅግ በጣም ፈሩ

Genesis 42:29

የአገሩ ጌታ

የግብጽ ጌታ

በቁጣ ተናገረን

በክፉ ንግግር ተናገረን

ሰላዮች እንደሆንን

ሰላዮች ሌላን አገር ለመጥቀም ሰለአንድ አገር በሚስጢር መረጃ የሚሰበስቡ ሰዎች ናቸው:: በዘፍጥረት 42 9 ሰላዮች የሚለውን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::እኛም እንዲህ አልነው እኛ የታመንን ሰዎች ነን፡፡ ሰላዮች አይደለንም፡፡ እኛ የአንድ አባት ልጆች የሆንን አሥራ ሁለት ወንድማማቾች ነን፡፡ እንዱ በሕይወት የለም …..በከነዓን ይገኛል ይህ በጥቅስ ውስጥ የሚገኝ ጥቅስ ይዞአል:: ይህም እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊጠቀስ ይችላል:: አት እኛ የታመንን ሰዎች እንጂ ሰላዮች አይደለንም:: እኛ የአንድ አባት ልጆች የሆንን አሥራ ሁለት ወንድማማቾች ነን:: አንዱ በሕይወት የለም … በከነዓን ይገኛል (በጥቅስ ውስጥ ያሉ ጥቅሶች ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

አንዱ በሕይወት የለም

“ወንድም” የሚለው ቃል የታወቀ ነው አት “አንዱ ወንድማችን በሕይወት የለም” (የተደበቁ ቃላትን የመግለጽ ዘይቤ ይጠቀሙ)

ታናሹም ….ዛሬ ከአባታችን ጋር አለ

“ወንድም” የሚለው ቃል የታወቀ ነው:: አት “ታናሽ ወንድማችን…. ዛሬ ከአባታችን ጋር አለ” (የተደበቁ ቃላትን የመግለጽ ዘይቤ ይጠቀሙ)

Genesis 42:33

የአገሩ ጌታ

የግብጽ ጌታ

ለተራቡት ቤተሰቦቻችሁ እህል ይዛችሁላችሁ ሂዱ

ቤቶች ቤተሰብን ይወክላሉ አት በራብ ወቅት ቤተሰባችሁን ለመርዳት እህል ይዛችሁላችሁ ሂዱ (ምትክ ቃላት ስለመጠቀም ይመልከቱ)

መንገዳችሁን ሂዱ

ወደ ቤታችሁ ሂዱ ወይም ሂዱ

እናንተም በምድሪቱ ትነግዳላችሁ

በምድሪቱ እንዲትሸጡና እንዲትገዙ እፈቅድላችኋለሁ

Genesis 42:35

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ እዚህ የተጠቀመው በታሪኩ ጠቃሚ ክሰተት ለማመልከት ነው በቋንቋዎ ይህን መግለጽ የማችሉበት መንገድ ካለ በዚህ ቦታ ሊጠቀሙ ይችላሉ

እነሆ እያንዳንዳቸው

ተገረሙ ምክንያቱም እያንዳንዳቸው

ልጅ አልባ አስቀራችሁኝ

ያለ ልጅ እኮ አስቀራችሁኝ ወይም ሁለቱን ልጆች እንዳጣ አደረጋችሁኝ

ይህ ሁሉ በእኔ ላይ ደረሰ

እነዚህ ሁሉ ጐዱኝ

Genesis 42:37

እርሱን በእጄ ስጠኝ

ይህ አብሮ እንዲሄድ ብንያምን እንዲሰጠውና በጉዞው እንደሚጠነቀቅለት ሮቤል የጠየቀው ጥያቄ ነው አት ለእርሱ ኃላፊነት ስጠኝ ወይም ለእርሱ እኔ ሊጠነቀቅለት ዘይቤያዊ አነጋገር ይጠቀሙ

ልጄ ወደዚያው አብሮአችሁ አይወርድም

ከከነዓን ወደ ግብጽ ጉዞ ስታሰብ እዚህ የተጠቀመው ወደታች መውረድ የሚለው አባባል የተለመደ ነው አት ልጄ ብንያምን አብሮአችሁ ወደ ግብጽ አይሄድም

ከእናንተ ጋር

እዚህ እናንተ ብዙን የሚያመለክትና የያዕቆብን ልጆች የሚገልጽ ነው( “እናንተ” አጠቃቀም ይመልከቱ)

ወንድሙ እንደሆነ ሞቶአል የቀረው እርሱ ብቻ ነው

የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “ባለቤቴ ራሔል ሁለትልጆች ነበራት ዮሴፍ ሞቶአልና ብንያም ብቻውን ቀርቶአል” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ስትሄዱ በመንገድ ላይ

“ወደ ግብጽ ስትሄዱና ስትመለሱ” ወይም “ርቃችሁ ስትሄዱ” እዚህ “መንገድ” “ጉዞን” ያመለክታል

ሽበቴን በመሪር ሐዘን ወደ መቃብር ታወርዱታላችሁ

ወደ መቃብር ታወርዱታለችሁ እንዲሞትና ወደ መቃብር እንዲወርድ ታደርጉታላችሁ የሚል አባባል ነው:: መቃብር በተለምዶ እንደሚታመነው ከምድር በታች ስለሆነ ታወርዱታላችሁ የሚለውን ቃል ይጠቀማል:: አት “እኔን ሽማግሌውን በሐዘን እንድሞት ታደርጉታላችሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሽበቴን

ይህ ያዕቆብን የሚያመለክትና ሽምግልና ዕድሜውን የሚገልጽ ነው አት “እኔ ሽማግሌ ሰው” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)


Chapter 43

1 አሁንም በምድሪቱ ላይ እንደጸና ነበር፤ 2 ከግብፅ ያመጡትንም እህል በልተው ከጨረሱ በኋላ፣ አባታቸው፣ “እስቲ እንደገና ወርዳችሁ፣ ጥቂት እህል ሸምቱልን” አላቸው። 3 ይሁዳ ግን እንዲህ አለው፤ “ ያ ሰው ወንድማችሁን ይዛችሁ ካልመጣችሁ ዳግመኛ ፊቴን ዐታዩም ብሎ በጥብቅ አስጠንቅቆናል፤ 4 ወንድማችን ከእኛ ጋር እንዲወርድ ከፈቀድህ ወደዚያ ሄደን እህል እንሸምትልሃለን፤ 5 እርሱን የማትልከው ከሆነ ግን እኛም ወደዚያ አንወርድም፤ ያም ሰው፣ ‘ወንድማችሁን ይዛችሁ ካልመጣችሁ ዳግመኛ ፊቴን ዐታዩም’ ብሎናል።” 6 እስራኤልም፣ “ሌላ ወንድም አለን ብላችሁ ለዚያ ሰው በመንገር ለምን ይህን ችግር እንዲደርስብኝ አደረጋችሁ?” ሲል ጠየቃቸው። 7 እነርሱም፣ “ሰውዬው ስለ ራሳችንና ስለ ቤተ ሰባችን አጥብቆ ጠየቀን፤ እንደገናም ‘አባታችሁ አሁንም በሕይወት አለ? ሌላስ ወንድም አላችሁ?’ ሲል ጠየቀን። እኛም ለጥያቄው መልስ ሰጠነው። ታዲያ፣ ‘ወንድማችሁን ይዛችሁ ወደዚህ እንድትመጡ’ እንደሚል እንዴት ማወቅ እንችል ነበር?” ብለው መለሱለት። 8 ይሁዳም አባቱን እስራኤልን እንዲህ አለው፣ “ልጁን ከእኔ ጋር ስደደው፤ እኛም በቶሎ እንሂድ፣ ይህ ከሆነ አንተም፣ እኛም፣ ልጆቻችንም አንሞትም፣ እንተርፋለን። 9 ስለ ልጁ ደኅንነት እኔ ራሴ ኃላፊ ነኝ፤ ስለ እርሱም በግል ተጠያቂ እሆናለሁ፤ እርሱንም በደኅና መልሼ ባላመጣውና እዚህ በፊትህ ባላቆመው ለዘላለም በደለኛ እኔ ልሁን። 10 ይህን ያህል ባንዘገይ ኖሮ፣ እስካሁን ሁለት ጊዜ ደርሰን መመለስ በቻልን ነበር።” 11 ከዚህ በኋላ አባታቸው እስራኤል እንዲህ አላቸው፤ “ነገሩ እንዲህ ከሆነስ ይህን አድርጉ፣ ምድሪቱ ከምታፈራቸው ምርጥ ነገሮች ጥቂት በለሳን፣ ጥቂት ማር፣ ሽቱ፣ ከርቤ፣ ተምርና ለውዝ በየስልቻችሁ ይዛችሁ ለዚያ ሰው ስጦታ ውሰዱለት። 12 በየስልቾቻችሁ አፍ ላይ የተገኘውን ብር መመለስ ስላለባችሁ፣ ዕጥፍ ገንዘብ ያዙ፤ ያ በየስልቾቻችሁ ውስጥ የተገኘው ብር ምናልባት በስሕተት የመጣ ሊሆን ይችላል። 13 ወንድማችሁንም ይዛችሁ ወደ ሰውዬው በቶሎ ሂዱ። 14 ሌላውን ወንድማችሁንና ብንያምን ይዛችሁ ለመመለስ እንድትችሉ ሁሉን የሚችል አምላክ በምሕረቱ የዚያን ሰው ልብ ያራራላችሁ። እኔ በበኩሌ ልጆቼን ካጣሁ፣ ባዶ እጄን መቅረቴ ነው።” 15 ስለዚህ ወንድማማቾቹ ገጸ በረከቱንና ዕጥፍ ገንዘብ ይዘው ከብንያም ጋር ወደ ግብፅ ለመሄድ ጉዞ ጀመሩ፤ እዚያም በደረሱ ጊዜ ዮሴፍ ፊት ቀረቡ። 16 ዮሴፍ ብንያምን ከወንድሞቹ ጋር ባየው ጊዜ የቤቱን አዛዥ፣ “እነዚህን ሰዎች ወደ ቤት ይዘሃቸው ሂድ፣ ዛሬ ቀትር ላይ አብረውኝ ስለሚበሉ አንድ ከብት እረድና አዘጋጅ” አለው። 17 አዛዡም ዮሴፍ የነገረውን አደረገ፣ ሰዎቹንም ወደ ዮሴፍ ቤት ወሰዳቸው። 18 ሰዎቹም ወደ ዮሴፍ ቤት በመወሰዳቸው ፈሩ፤ እነርሱም፣ “ወደዚህ የመጣነው ቀደም ሲል እዚህ መጥተን ስንመለስ በየስልቾቻችን ውስጥ ተመልሶ በተጨመረው ብር ሰበብ ነው። ሰውዬው ሊያስረንና ባሪያዎች ሊያደርገን አህዮቻችንንም ሊወስድ ይችላል።” 19 ወደ ዮሴፍ ቤት አዛዥ ቀርበው፣ በቤቱ መግቢያ ላይ አነጋገሩት፤ 20 እንዲህም አሉት፤ “ለመጀመሪያ ጊዜ እህል ለመሸመት ወደዚህ መጥተን ነበር፤ 21 ነገር ግን ለአዳር በሰፈርንበት ቦታ የየስልቾቻችንን አፍ ስንከፍት እያንዳንዳችን በስልቾቻችን አፍ ላይ ብራችንን ሙሉውን አገኘነው። ገንዘቡንም ይኸው መልሰን ይዘን መጥተናል። 22 አሁንም እህል መሸመት የሚሆነን ተጨማሪ ብር ይዘን መጥተናል፤ በዚያን ጊዜ ገንዘቡን በየስልቾቻቸን ውስጥ ማን መልሶ እንዳስቀመጠው ግን አናውቅም” አሉት። 23 የቤቱ አዛዥም፣ “አይዞአችሁ አትፍሩ፣ በየስልቾቻችሁ ውስጥ ያገኛችሁትን ገንዘብ የሰጣችሁ የእናንተም የአባቶቻችሁም አምላክ ነው፤ እኔ እንደሆንሁ ብሩን ተቀብያለሁ” አላቸው። ከዚያም ስምዖንን አውጥቶ አገናኛቸው። 24 የቤቱ አዛዥ ሰዎቹን ወደ ዮሴፍ ቤት አስገብቶ እግራቸውን የሚታጠቡበት ውሃ አቀረበላቸው፤ ለአህዮቻቸውም የሚበሉት ገፈራ ሰጣቸው። 25 ምሳ በዚያ እንደሚበሉ ተነገሯቸው ስለነበር፣ ዮሴፍ በቀትር ከመግባቱ በፊት እጅ መንሻዎቻቸውን ለማበርከት ተዘጋጁ። 26 ዮሴፍም ወደ ቤቱ ሲገባ የመጧቸውን ስጦታዎች አበረከቱለት፤ ወደ መሬት ዝቅ ብለውም እጅ ነሡት። 27 ዮሴፍም ስለ ደኅንነታቸው ጠየቃቸው፣ ከዚያም፣ “ሽማግሌ አባት እንዳላችሁ ነግራችሁኝ ነበር፤ ደኅና ነው? አሁንም በሕይወት አለ?” አላቸው። 28 እነርሱም መልሰው፣ “አገልጋይህ አባታችን አሁንም በሕይወት አለ፤ ደኅና ነው” በማለት ወደ መሬት ዝቅ ብለው እጅ ነሡት። 29 ዮሴፍ በዓይኑ ሲቃኝ የእናቱን ልጅ ብንያምን ዐየና፣ “ያ የነገራችሁኝ ታናሽ ወንድማችሁ ይህ ነው?” ብሎ ጠየቃቸው። ብንያምንም፣ “ልጄ እግዚአብሔር ይባርክህ” አለው። 30 ዮሴፍ ወንድሙን በማየቱ ስሜቱ በጥልቅ ስለተነካ፣ ፈጥኖ ከፊታቸው ገለል አለ፤ ሰውር ያለ ቦታም ፈልጎ፣ ዕልፍኙ ውስጥ አለቀሰ። 31 ፊቱንም ከታጠበ በኋላ ወጣ፤ ስሜቱንም በመቆጣጠር ምሳ እንዲቀርብ አዘዘ። 32 ለዮሴፍ ለብቻው ቀረበለት ለወንድሞቹም ለብቻቸው ቀረበላቸው፤ እንዲሁም ከእርሱ ጋር ለሚበሉት ግብፃውያን ደግሞ ሌላ ገበታ ቀረበላቸው፤ ምክንያቱም ግብፃውያን ከዕብራውያን ጋር አብሮ መመገብን እንደጸያፍ ይቆጥሩት ነበር። 33 ወንድማማቾቹ ከታላቁ አንስቶ እስከታናሹ እንደየዕድሜአቸው በዮሴፍ ፊት በተርታ ተቀምጠው ነበር፤ በመገረምም እርስ በርሳቸው ተያዩ። 34 ከዮሴፍ ገበታ ላይ እየተነሣ ለእያንዳንዳቸው ምግብ ሲቀርብ የብንያም ድርሻ ከሌሎቹ አምስት ዕጥፍ ነበር። እነርሱም እንዲህ ባለ ሁኔታ አብረውት ተደሰቱ እስኪረኩም ጠጡ።



Genesis 43:1

ራቡ በምድሪቱ ላይ እንደጸና ነበር

ከነዓን የሚለው ቃል የታወቀ ነው ይህ ሃሳብ ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት በከነዓን ምድር ራቡ የጸና ነበር (ድብቅ ቃላትን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ የተጠቀመው የታሪኩን አድስ ክፍል መጀመሩን ለማመልከት ነው በቋንቋዎ ይህን መግለጽ የሚችሉበት መንገድ ካለ ይጠቀሙ (አድስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

በልተው ከጨረሱ በኋላ

ያዕቆብና ቤተሰቡ በልተው ከጨረሱ በኋላ

ያመጡትን

የያዕቆብ ታላቅ ልጆች ያመጡትን

ለኛ ሸምቱልን

እዚህ እኛ ያዕቆብን የያዕቆብን ልጆችና የቀሩ የቤተሰብ አባላትን ያመለክታል:: (ሁሉን አካታች “እኛ” ይመልከቱ)

Genesis 43:3

ይሁዳ እንዲህ አለው

ይሁዳ ለአባቱ ለያዕቆብ እንዲህ አለው

ያ ሰው

ይህ ዮሴፍን ነው የሚያመለክተው ነገር ግን ወንድምቹ ዮሴፍ መሆኑን አላወቁትም ነበር:: እነርሱም እርሱን ያመለከቱን እንደ “ያ ሰው” ወይም በዘፍጥረት 42:3ዐ እንደተነገረው “ያ ሰው የምድሪቱ ጌታ” ነው::

ወንድማችሁን ይዛችሁ ካልመጣችሁ ፊቴን አታዩም ብሎ አስጠንቀቆናል

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ ይዞአል ይህም እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ታናሽ ወንድማችንን ይዘነው ካላመጣን ፊቱን ማየት እንደማንችል አስጠንቅቆናል” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

በጥብቅ አስጠንቅቆናል

እንዲህም በማለት በጥብቅ አስጠንቀቆናል

ፊቴን አታዩም

ወደ ግብጽ አገር ያለ ብንያም መመለስ እንደማይችሉ ለአባቱ ለማጽናት በዘፍጥረት 43፡ 4-5 ይሁዳ ይህን ሀረግ ሁለት ጊዜ ይጠቀማል:: ፊቴን የሚለው የዚያ ሰው የዮሴፍ ፊት ያመለክታል:: አት “ፊቴን አታዩም” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዜይቤ ይጠቀሙ)

ወንድማችን ከእኛ ጋር

ይሁዳ ራሔል ከመሞትዋ በፊት የወለደችውን የመጨረሻ ልጅ ብንያምን ያመለክታል

እኛም ወደዚያ አንወርድም

ከከነዓን ወደ ግብጽ ጉዞ በሚነገርበት ጊዜ “ወደታች መውረድ” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነው

Genesis 43:6

ለምን በደላችሁኝ?

ለምን ይህ ችግር እንዲደርስብኝ አደረጋችሁ?

ሰውየው አጥብቆ ጠየቀን

ሰውየው ብዙ ጥያቄዎችን ጠየቀን

ስለእኛ

እዚህ እኛ የሚለው በተለይ የሚያመለክተው ወደ ግብጽ የወረዱና ከሰውየው ጋር የተነጋገሩ ወንድሞችን ነው

አባታችሁ አሁን በሕይወት አለ? ሌላ ወንድም አላችሁ? ሲል ጠየቀን

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስን ይዞአል እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊጠቀስ ይችላል አት አባታችን በሕይወት እንዳለና ሌላ ወንድም እንዳለን በቀጥታ ጠይቆናል:: (በጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

እኛም ለጥያቄዎቹ መልስ ሰጠን

የጠየቀንን ጥያቄዎች መለስንለት

…ይዛችሁ እንዲትመጡ እንደሚለን እንዴት ማወቅ እንችል ነበር?

ሰውየው ምን ማድረግ እንዳለባቸው እንደሚነግር ልጆቹ አለማወቃቸውን አጽንተው ለመንገር ጥያቄ ይጠቀማሉ ይህ አግናኝ ጥያቄ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊተረጐም ይችላል አት እንደዚህ … እንደሚለን አላወቅንም ነበር (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ወንድማችሁን ይዛችሁ ውረዱ ወይም አምጡ እንደሚለን

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስን ይዞአል እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል አት ወንድማችንን የዘን ወደ ግብጽ እንድንወርድ እንደሚነግረን (በጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ወንድማችሁን ይዛችሁ ውረዱ

ከከነዓን ወደ ግብጽ ጉዞ በሚነገርበት ጊዜ “ወደታች መውረድ” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነው

Genesis 43:8

እኛና አንተ ልጆቻችንም ደግሞ እንድንድን እንዳንሞትም

እንድንድን እና እንዳንሞት የሚሉ ሀረጐች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: ይሁዳም በሕይወት ለመኖር ከግብጽ አህል መሸመት እንዳለባቸው በማጽናት ይናገራል:: አት “መላው ቤተሰባችን እንዲተርፍ ወደ ግብጽ ወርደን እህል መሸመት ይገባናል” (ተመሣሣይ ተጓዳኝ ንጽጽር ይመልከቱ)

እኛም ተነሥተን

እዚህ እኛ ወደ ግብጽ የሚጓዙ ወንድሞችን ያመለክታል:: (የሚያቅፍና የማያቅፍ እኛ ይመልከቱ)

እኛ እንተርፋለን

እዚህ “እኛ” ወንድሞች እስራኤልና መላውን ቤተሰብ ያመለክታል (የሚያቅ “እኛ” ይመልከቱ)

እኛ ሁለታችን

እዚህ እኛ ወንድማማቾችን ያመለክታል (የሚያቅፍና የማያቅፍ “እኛ” ይመልከቱ)

እኛ አንተም

እዚህ አንተ በነጠላ የተገለጸና እስራኤልን ያመለክታል (ሁለተኛ ወገን ሰው ወይም አንተ አጠቃቀም ይመልከቱ)

የእኛም ልጆች ወይም ልጆቻችን

እኛ ወንድሞችን ያመለክታል በረሀቡ ጊዜ ሊሞቱ የሚችሉ ትናንሽ ልጆችን ያመለክታል

እኔ ዋስ እሆንለታለሁ

“ዋስ” የተባለው ረቂቅ ስም እንደ “ተስፋ” የተባለው ግሥ ሊገለጽ ይችላል፡፡ (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

ተጠያቂ እሆናለሁ

ያዕቆብ ይሁዳን እንዴት ተጠያቂ እንደሚያደረገው በግልጽ መነገር አለበት አት በብንያም ላይ በሚደርሰው ነገር ሁሉ ምላሽ እንዲሰጥ ታደርገኛለህ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይጠቀሙ)

እኔ ራሴ ኃላፊነትን እሸከማለሁ

ይህ አንድ ሰው እንደሚሸከመው ዕቃ ተደርጐ ኃላፊነትን መሸከም ይገልጻል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ባንዘገይ ኖሮ

ይሁዳ ቀድሞ መደረግ የነበረበት ነገር ግን ያልተደረገውን ነገር ይገጻል ተጨማሪ እህል ለመሸመት ልጆቹ ወደግብጽ ሳይሄዱ በመቆየታቸው አባቱን እንስራኤልን ይሁዳ በመውቀስ ይናገረዋል (የሚገመቱ ታሳቢ ሁኔታዎችን ይመልከቱ)

እስካሁን ሁለት ጊዜ ደርሰን መመለስ በቻልን

ሁለት ጊዜ መመላለስ በቻልን

Genesis 43:11

እንዲህ ከሆነ ይህን አድርጉ

ይህ ብቸኛ ምርጫችን ከሆነ ይህን አድረጉ

ተሸክማችሁ ውረዱ

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ መውረድ የሚለውን ቃል መጠቀም የተለመደ ነበር

በለሳን

ቆዳን ለማከምና ለመከላከል የሚጠቀሙበት ጣፊጨነት ያለው ቅባታማ ፍሬ ነው:: በዘፍጥረት 37:25 ይህን ቃል እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት “መድኃኒት”

ቅመማ ቅመሞች

የተለያዩ ቅመማ ቅመሞች በዘፍጥረት 37:25 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

ለውዝ

ትናንሽ አረንጓዴ ተክል ለውዞች (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ተምር

ጣፋጭ ጣዕም ያለው የዛፍ ፍሬ (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በእጃችሁ ዕጥፍ ገንዘብ ያዙ

እዚህ “እጅ” ሙሉ ሰውን ይወክላል አት ዕጥፍ ገንዘብ ውሰዱ (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በየስልቾቻችሁ አፍ የተገኘውን የተመለሰውን ብር በአጠፌታ አድርጋችሁ በእጃችሁ ውሰዱ

እዚህ እጅ ሙሉ ሰውን ይወክላል በስልቼቻችሁ አፍ የተመለሰው ብር የተባለው ሀረግ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “አንድ ሰው በስልቾቻችሁ የጨመረውን ብር መልሳችሁ ወደ ግብጽ ውሰዱ” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤና ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 43:13

ወንድማችሁንም ውሰዱ

ብንያምንም ደግሞ ውሰዱ

ሂዱ

ተመለሱ

ሁሉም የሚችል አምላክ በዚያ ሰው ፊት ምሕረትን ይሰጣችሁ

ምሕረት የሚለው ረቂቅ ስም ርኀራኄ በሚለው ቅጽል ሊተረጐም ይችላል:: አት “ሁሉን የሚችል አምላክ ያ ሰው እንዲራራ ያድርግላችሁ” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

ሌላውንም ወንድማችሁንም

ስምዖንን

እኔም ልጆቼን እንዳጣሁ አጣሁ

ልጆቼን ካጣሁ ያው አጣሁ ያዕቆብ ልጆቹን ቢያጣ እንዳጣ ሊቀበል አውቆታል ማለት ነው

በእጃቸው … ወሰዱ

እዚህ “እጅ” ሙሉ ሰውን ይወክላል:: አት እነርሱም … ወሰዱ (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ወደ ግብጽም ወረዱ

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደዚያ ወረደ” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነበር

Genesis 43:16

ከራሳቸው ጋር ብንያምን

ብንያም ከዮሴፍ ታላቅ ወንድሞች ጋር

የቤቱን አዛዥ

የቤቱ አዛዥ የዮሴፍን ቤት ተግባራትን ለማሰተዳደር ኃላፊነት ነበረው

እነዚህን ሰዎች አመጣቸው

እዚህ “አመጣቸው” እንደ “ወሰዳቸው” ሊተረጐም ይችላል:: (“መጣ” እና “ሄደ” አጠቃቀም ይመልከቱ)

ወደ ዮሴፍ ቤት

ወደ ዮሴፍ ቤት ውስጥ

Genesis 43:18

ሰዎቹም ፈሩ

የዮሴፍ ወንድሞች ፈሩ

ወደ ዮሴፍ ቤት ስለተወሰዱ

ይህ ተሻጋሪ ግስ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፤ አት “ወደ ዮሴፍ ቤት ይሄዱ ነበር” ወይም “የቤቱ አዛዥ ወደ ዮሴፍ ቤት ይወስዳቸው ነበር” (ተሻጋሪና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)፡፡

ቀደም ስል እዚህ መጥተን ስንመለስ በየስልቾቻችን ውስጥ ተመልሶ በተጨመረው ብር ሰበብ ነው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት የቤቱ አዛዥ እየወሰደን ያለው ያነ አንድ ሰው በስልቾቻችን በጨመረው ብር ሰበብ ነው (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ሰውዬው በዚህ አጋጣሚ ሊተነኰልብን ይሆናል ሊያሥረንም ይችላል

ይህ እንደ አድስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: አት “ሊከሰን እጋጣሚ እየጠበቀ ስላለ ሊያሰረን ይሆናል”

Genesis 43:21

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

ወንድሞቹ ለቤቱ አዛዥ መናገር ቀጠሉ

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረገ በታሪኩ ዋና ክተት ለማመልከት ተጠቅሞአል በቋንቋዎ ይህን የሚገልጹበት መንገድ ካለ ይጠቀሙ::

ወደምናድርበት ቦታ በደረስን ጊዜ

ለአዳር በሠፈርንበት ቦታ በደረስን ጊዜ

እነሆ

እዚህ “እነሆ” የሚለው ቃል ወንድሞቹ ባዩት ነገር እንደተገረሙ ለማሳየት ተጠቅሞአል::

እያንዳንዳችን በስልቾቻችን አፍ ብራችንን ሙሉውን አገኘነው

እያንዳንዳችን በየስልቾቻችን ሙሉውን ብሮቻችንን አገኘው

መልሰን በእጃችን አመጣነው

እዚህ እጆች ሙሉውን ሰው ይወክላሉ አት ብሮቻችንን መልሰን የዘነው መጣን (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ደግሞም እህል መሸመቻ የሚሆነንን ተጨማሪ ገንዘብ ይዘን መጥተናል/ወርደናል

እዚህ እጆች ሙሉ ሰው ይወክላሉ:: አት “ደግሞም እህል መሸመቻ የሚሆነንን ብር ይዘን መጥተናል” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ይዘን ወርደናል

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደዚያ ወረደ” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነበር

ሰላም ለእናንተ ይሁን

ረቂቅ ስም ሰላም እንደ ግሥ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ዘና በሉ ወይም ተረጋጉ” (ረቂቅ ስሞችን ይመልከቱ)

አምላካችሁና የአባታችሁ አምላክ

የቤቱ አዛዥ ሁለት የተለያዩ አምላኮችን እየተናገረ አይደለም አት “አምላካችሁ አባታችሁ የሚያመለከው”

Genesis 43:24

እግሮቻቸውን የሚታጠቡበት

ይህ ባህል ረጅም ጉዞ ተጉዘው ከመጡ በኋላ የደከሙ መንገደኞች ድካማቸው እንዲቀል የሚረዱበት ነው:: የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልክቱ)

ለአህዮቻቸው የሚበሉትን ገፈራ ሰጣቸው

ገፈራ ለከበቶች የሚሆን ድርቆሽ ነው

Genesis 43:26

በእጃቸው ያመጡአቸውን እጅ መንሻዎች አበረከቱለት

“እጅ” ሙሉን ሰው ይወክላል:: አት “ወንድሞች ያመጡአቸውን እጅ መንሻቸውን” (ክፍልን እንደሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በፊቱም ወድቀው ሰገዱለት

ይህ ክብርና አክብሮት የሚገለጽበት መንገድ ነው:: (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Genesis 43:28

አገልጋይህ አባታችን

አባታቸውን እንደ “አገልጋይህ” ማመልከታቸው አክብሮታቸውን ለማሳየት ነው አት “አባታችን የሚያገለግልህ”

አጐንብሰው ሰገዱለት

እነዚህ ቃላት በመሠረቱ ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው በሰውየው ፊት ጐንበስ በማለት አክብሮታቸውን ገለጹ:: አት “በፊቱ ሰገዱለት” (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

ዮሴፍም ዐይኑን ሲቃኝ

ቀና ብሎ ሲመለከት ማለት ነው ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ

የእናቱን ልጅ እናም አለ

ይህ በአድስ ዐረፍተ ነገር መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት “የእናቱን ልጅ.. አየ:: ዮሴፍም አለ፤”

ታናሽ ወንድማችሁ ይህ ነውን?

ተገቢ አማራጭ ትርጉሞች 1 ይህ ሰው ብንያምን እንደሆነ ለማረጋገጥ ዮሴፍ በውኑ ይጠይቃቸዋል ወይም 2) ይህ አግናኝ ጥያቄ ነው:: “ደግሞ ይህ ታናሽ ወንድማችሁ …. “ (አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ልጄ

ይህ አንድ ሰው በዝቅተኛ ደረጃ ላለ ሌላ ሰው በጓደኝነት መንገድ የሚጠራው አጠራር ነው:: አት “ወጣቱ”

Genesis 43:30

ፈጥኖ ከክፍሉ ወጣ

ተቻኩሎ ከክፍሉ ወጣ

ወንድሙን በማየቱ ስሜቱ በጥልቅ ስለተነካ

ስሜቱ በጥልቀት የሚለው ሀረግ አንድ መልካም ነገር ሲከሰት የሚሰማ ታላቅ ስሜትን ያመለክታል:: አት “ለወንድሙ የመራራት ጠንካራ ስሜት ነበረው” ወይም “ለወንድሙ ጠንካራ የናፍቆት ስሜት ነበረው” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አለ

ዮሴፍ እንደሚናገር ግልጽ ማድረግ ይቻላል:: አት “እናም ለአገልጋዮቹ አላቸው” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ማዕድ ይቅረብ

ሰዎች እንዲመገቡ ምግብን ማቅረብ ማለት ነው፡፡

Genesis 43:32

አገልጋዮችም ለዮሴፍ ለብቻው ለወንድሞቹም ለብቻቸው አቀረቡላቸው:: ከእርሱ ጋር ለሚበሉ ግብጻዊያን ደግሞ ለብቻቸው አቀረቡላቸው::

ይህም ዮሴፍ ወንድሞቹና ሌሎች በአንድ ክፍል በተለያየ ቦታ ተቀምጠው ይመገባሉ ማለት ነው አገልጋዮችም ለዮሴፍ ለብቻው ለመንድሞቹም ለብቻቸው እናም ከእርሱ ጋር ለሚበሉ ግብጻዊያን ደግሞ ለብቻቸው አቀረቡላቸው

ከእርሱ ጋር ለሚበሉ ግብጻዊያን ለብቻቸው

እነዚህ ምናልባት ከእርሱ ጋር የሚበሉ የግብጽ ባለሥልጣናት ይሆናሉ ነገር ግን ከዮሴፍና ከዕብራዊያን ወንድሞቹ ተለይተው ተቀምጠዋል

ግብጻዊያን ከዕብራዊያን ጋር መመገብ አይሆንላቸውም ምክንያቱም ያ ለግብጻዊያን መርከስ ነውና

ይህ እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ሊገለጽ ይችላል ይህንን ያደረጉበት ምክንያት ግብጻዊያን ከዕብራዊያን ጋር መመገብ ጸያፍ አድርገው ያስባሉ

አብረው እንጀራ አይበሉም

እዚህ እንጀራ ጠቅላላ ምግብ ይወክላል (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ወንድምቹ በእርሱ ፊት ተቀመጡ

እያንዳንዱ ወንድም የት መቀመጥ እንዳለበት ዮሴፍ እንዳዘጋጀ ሊገመት ይገልጻል የተገለጸውን መረጃ ግልጽ ማድረግ ይቻላል አት የሚቀመጡበት ቦታ በተዘጋጀላቸው መሠረት በሰውየው/ዮሴፍ ፊት ወንድሞቹ ተቀመጡ (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይጠቀሙ)

በፊቱም በኩሩ እንደታላቂነቱ ታናሹም እንደታናሽነቱ

“በኩር”ና “ታናሽ” የተጠቀሙት ሁሉም ወንድሞች በአንድነት እንደየዕድሜያቸው በተርታ እንደተቀመጡ ለመግለጽ ነው::( ነጠላ ነገር በብዙ የመግለጽ ዘይቤ/merism/ ይመልከቱ)

ሰዎቹም/ወንድሞቹም በአንድነት ተገረሙ

ይህን ባወቁ ጊዜ ሰዎቹ በጣም ተገረሙ

የብንያም ድርሻ ከሌሎች ወንድሞች አምስት እጥፍ ነበር

አምስት እጥፍ የሚለው ሀረግ በአጠቃላይ ብዙ በሚለው ሊገለጽ ይችላል:: አት “ብንያም የተቀበለው ድርሻ ወንድሞቹ ከተቀበሉት በጣም ብዙ ነበር”


Chapter 44

1 ከዚህ በኋላ ዮሴፍ ለቤቱ አዛዥ እንዲህ ሲል መመሪያ ሰጠው፤ የሰዎቹ ስልቻ የሚይዘውን ያህል እህል በየስልቻቸው ሙላላቸው፤ የእያንዳንዱንም ገንዘብ በየስልቻው አፍ አስቀምጠው። 2 ከዚያም የብር ዋንጫዬን በታናሹ ወንድማቸው ስልቻ አፍ ከእህሉ ዋጋ ጋር ጨምረው።” አዛዡም ዮሴፍ እንዳለው አደረገ። 3 ጠዋት በማለዳ ወንድማማቾቹ አህዮቻቸውን ይዘው እንዲሄዱ ተደረገ። 4 ከከተማውም ምንም ያህል ርቀው ሳይሄዱ፣ ዮሴፍ የቤቱን አዛዥ እንዲህ አለው፤ “እነዚያን ሰዎች ቶሎ ድረስባቸውና፣ ‘በመልካም ፋንታ ክፉ የመለሳችሁት ስለ ምንድን ነው? 5 የጌታዬን የብር ዋንጫ የሰረቃችሁት ለምንድነው? ዋንጫው ጌታዬ የሚጠጣበትና ሁሉን ነገር መርምሮ የሚያውቅበት እንደሆነ አታውቁምን? ይህ ያደረሳችሁት በደል እጅግ ከባድ ነው’ ብለህ ነገራቸው።” 6 የቤቱ አዛዥም እንደደረሰባቸው፣ ልክ እንደተባለው ተናገራቸው። 7 እነርሱ ግን እንዲህ አሉት፤ “ጌታችን እንዲህ ያለ ነገር ለምን ይናገራል? እኛ አገልጋዮችህ እንዲህ ያለውን ነገር አናደርገውም። 8 ከዚህ ቀደምም በየስልቾቻችን አፍ የተገኘውን ብር ከከነዓን እንኳ መልሰን አምጥተናል፤ ታዲያ አሁን ብር ወይም ወርቅ ከጌታህ ቤት እንዴት እንሰርቃለን? 9 የጠፋው ዕቃ ከአገልጋዮችህ የተገኘበት ይሙት፤ የቀረነው የጌታችን ባሮች እንሁን።” 10 አዛዡም መልካም ነው፤ እንዳላችሁት ይሁን፤ ጽዋው የተገኘበት ሰው ባሪያዬ ይሆናል፤ የቀራችሁት ግን ከበደል ነጻ ትሆናላችሁ” አላቸው። 11 ስለዚህ በፍጥነት ስልቻዎቻቸውን አወረዱ፤ እያንዳንዱም የራሱን ስልቻ ከፈተ። 12 ከዚያም አዛዡ ፍተሻውን ከታላቁ ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ቀጠለ። በመጨረሻም ጽዋው በብንያም ስልቻ ውስጥ ተገኘ። 13 በዚህ ጊዜ ልብሶቻቸውን በሐዘን ቀደዱ፤ ሁሉም ስልቾቻቸውን በየአህዮቻቸው ጭነው ወደ ከተማይቱ ተመለሱ። 14 ይሁዳና ወንድሞቹ ወደ ዮሴፍ ቤት ሲገቡ፣ ዮሴፍ ገና ከቤቱ አልወጣም ነበር። እነርሱም በፊቱ ተደፍተው ሰገዱ። 15 ዮሴፍም፣ “ለምን እንዲህ ያለ ነገር አደረጋችሁ? እንደ እኔ ያለ ሰው ስውር ነገርን የሚያውቅበት ልዩ ጥበብ እንዳለው አታውቁምን?” ሲል ጠየቃቸው። 16 ይሁዳም፣ “ከእንግዲህ ለጌታችን ምን ማለት እንችላለን? ምንስ እንመልሳለን? እንዲህ ካለው በደል ንጹሕ መሆናችንን ማስረዳትስ እንዴት ይቻለናል? ምክንያቱም እግዚአብሔር የሠራነውን በደል ገልጦታል፤ እንግዲህ ዋንጫው የተገኘበት ሰው ብቻ ሳይሆን ሁላችንም ባሪያዎችህ እንሁን” አለ። 17 ዮሴፍም፣ “ይህንስ አላደርገውም፣ ዋንጫው የተገኘበት ሰው ብቻ የእኔ ባሪያ መሆን አለበት፤ ሌሎቻችሁ በሰላም ወደ አባታችሁ መመለስ ትችላላችሁ” አለ። 18 ይሁዳም ወደ ዮሴፍ ቀረብ ብሎ፣ “ጌታዬ ሆይ፣ እኔ አገልጋይህ አንዲት ቃል ብቻ ልናገር፣ ምንም እንኳ የፈርዖን ያህል የተከበርክ ብትሆንም እባክህ አትቆጣኝ። 19 ጌታዬ፣ ‘አባት ወይም ወንድም አላችሁ?’ ብሎ አገልጋዮቹን ጠይቆ ነበር። 20 እኛም፣ ‘አዎን ሽማግሌ አባት አለን፤ አባታችንም በስተርጅና የወለደው ትንሽ ልጅ አለው፣ ወንድምዬው ሞቶአል፣ ከአንድ እናት ከተወለዱት ልጆች መካከል የተረፈው እርሱ ብቻ ነው፤ አባቱም በጣም ይወደዋል’ ብለንህ ነበር። 21 ከዚያም አንተ አገልጋዮችህን፣ ‘እንዳየው ወደ እኔ አምጡት’ አልኸን። 22 እኛም ለጌታዬ፣ ‘ልጁ ከአባቱ ሊለይ አይችልም፤ ከተለየው ደግሞ አባትዬው ይሞታል’ አልንህ። 23 አንተ ግን እኛን አገልጋዮችህን፣ ‘ታናሽ ወንድማችሁ አብሮአችሁ ወደዚህ ካልመጣ ዳግመኛ ፊቴን ዐታዩም’ አልኸን። 24 እኛም ወደ አገልጋይህ ወደ አባቴ በተመለስን ጊዜ አንተ ጌታዬ ያልኸንን ነገርነው። 25 ከዚያም አባታችን፣ ‘እስቲ ተመልሳችሁ ጥቂት እህል ሸምቱልን’ ሲለን 26 ‘መሄድ አንችልም፤ መሄድ የምንችለው ታናሽ ወንድማችን አብሮን ሲሄድ ብቻ ነው። ታናሽ ወንድማችንን ይዘን ካልሄድን በስተቀር የሰውዬውን ፊት ማየት አንችልም’ አልነው። 27 አገልጋይህ አባቴም እንዲህ አለን፤ ‘ሚስቴ ሁለት ወንዶች ልጆች እንደወለደችልኝ ታውቃላችሁ፤ 28 አንዱ በወጣበት በመቅረቱ በእርግጥ አውሬ በልቶት ይሆናል አልሁ፣ ከዚያ በኋላ ዐላየሁትም። 29 አሁን ደግሞ ይህን ልጅ ወስዳችሁ አንዳች ጉዳት ቢደርስበት ሽበቴን በመራር ሐዘን ወደ መቃብር ታወርዱታላችሁ።’ 30 እንግዲህ አሁን ልጁን ሳንይዝ ወደ አገልጋይህ ወደ አባቴ ብመለስ ሕይወቱ ከልጁ ሕይወት ጋር በጥብቅ የተሳሰረ ስለሆነ፣ 31 የልጁን ከእኛ ጋር አለመኖር ሲያይ አባቴ ይሞታል። ከዚህም የተነሣ እኛ አገልጋዮችህ የአባታችንን ሽበት በመሪር ሐዘን ወደ መቃብር እናወርደዋለን። 32 እኔ አገልጋይህ፣ “ልጅህን መልሼ ሳላመጣ ብቀር ለዘላለም በደለኛ አድርገህ ቁጠረኝ’ በማለት ስለ ልጁ ደህንነት በአባቴ ፊት ራሴን ዋስ አድርጌአለሁ። 33 ስለዚህ አሁን፣ አገልጋይህ በልጁ ፋንታ የአንተ የጌታዬ ባሪያ ሆኜ እዚሁ ልቅር ልጁ ግን ከወንድሞቹ ጋር ይመለስ። 34 ልጁን ሳልይዝ እንዴት ተመልሼ ወደ አባቴ እሄዳለሁ? እባክህ በአባቴ ላይ የሚደርሰውን መከራ እንዳይ አታድርገኝ።”



Genesis 44:1

አጠቃላይ መረጃ

ይህ በታሪኩ አድስ ክስተት ይጀምራል ይህ በተለይ ከግብዣው ሁለተኛው ቀን ማግሥት የተከሰተውን ያመለክታል፡፡

የቤቱ አዛዥ

የቤቱ አዛዥ የዮሴፍ ቤት ተግባራትን ለማስተዳደር ኃላፊነት ያለው ነበር

የሁሉም ሰው ገንዘብ

የእነርሱ ገንዘብ በትንሽ ቦርሳ ውስጥ የተቀመጡ የብር ሳንቲሞች ነበሩ

በስልቻው አፍ

በስልቻው

ዋንጫየን የብሩን ዋንጫዬን… ጨምረው

የብሩን ዋንጫዬን ጨምረው

በታናሹ ወንድማቸው ስልቻ አፍ

ወንድም የሚለው ቃል የታወቀ ነው አት በታናሽ ወንድማቸው ስልቻ (ድብቅ ቃላትን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 44:3

ጎህ ሲቀድ

የማለዳ ብርሃን ሲወጣ

ሰዎቹ ከነአህዮቻቸው ተሸኙ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ሰዎችን ከነአህዮቻቸው ሸኙአቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ለበጎ ነገር ስለምን ክፉ መለሳችሁ?

ይህ ጥያቄ ወንድሞቹን ለመቆጣት ተጠቅሞአል:: አት እኛ “ለእናንተ መልካም ካደረግን በኋላ ክፉ መለሳችሁብን” (ሽንገላ አዘል/ rhetorical/ ጥያቄ ይመልከቱ)

ይህ ጌታዬ የሚጠጣበት የተሰወረ ነገርም የሚያውቅበት ጽዋ አይደለምን?

ይህ ጥያቄ የተጠቀመው ወንድሞቹን ለመቆጣት ነው፡፡ አት “ይህ ጽዋ ጌታዬ የሚጠጣበትና የተሰወረ ነገርንም የሚያውቅበት እንደሆነ በእርግጥ ታውቃችሁ” (ሽንገላን የያዘ ጥያቄ ይመልከቱ) ይህ ያደረጋችሁት የፈጸማችሁት ድርጊት ክፉ ነው ያደረጋችሁት የሚለውን መደጋገሙ ትኩረት ለመስጠት ነው አት የፈጸማችሁት ነገር እጅግ ክፉ ነው ተመሣሣይ ተጓዳኝ ንጽጽር ነው::

Genesis 44:6

ይህንም ቃል ነገራቸው

ዮሴፍ የነገራቸው የነገረውን ነገራቸው

ጌታዬ እንደዚህ ያለውን ቃል ለምን ይናገራል?

“ቃል” የተናገረውን ነገር:: ይወክላል ወንድሞቹ የቤቱን አዛዥ እንደ “ጌታዬ” ያመለክታሉ:: ይህ በከፍተኛ ኃላፊነት ላሌ ሰው የሚነገር መደበኛ አባባል ነው:: አት “ጌታዬ ለምን እንደዚህ ይናገራሉ?” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤና አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ይህን ነገር ማድረግ ከባሪያዎችህ ይራቅ

አንድ ሰው አንድን ነገር የማያደርገው ያ ሰው አንድን ዕቃ ከራሱ አርቆ እንደማስቀመጥ ተደርጐ ተገልጾአል፣ (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 44:8

እነሆ…ብር

“እኛ ስለምንናገረው ነገር ያድምጡ እናም የምንናገረው ነገር እውነት እንደሆነ ያያሉ፤ ብሩ”

በየስልቾቻችን አፍ የተገኘውን ብር

“በየስልቾቻችን ያገኘነውን ብር ያውቃሉ”

ከከነዓን አገር መልሰን ወደ አንተ አምጥተናል

ከከነዓን መልሰን ወደ አንተ አምጥተናል

ታዲያ ብር ወይም ወርቅ ከጌታህ ቤት እንዴት እንሰርቃለን?

ወንድምቹ ከግብጽ ጌታ እንዳልሠረቁ እትኩሮት ለመስጠት ጥያቄ ይጠቀማሉ:: አት “ስለዚህ ከጌታህ ቤት የወሰድነው ምንም ነገር የለም!” (ሽንገላ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

ብር ወይም ወርቅ

እንዚህ በጣምራ ቃላት የተጠቀሙት ዋጋ ያለውን ምንም ነገር እንዳልሠረቁ ለመግለጽ ነው

ከአገልጋዮችህ ይህ የተገኘበት

ወንድምች ራሳቸውን እንደ “የአንተ አገልጋዮች” ይገልጻሉ:: ይህ ከፍተኛ ስልጣን ላለ ሰው የሚነገር መደበኛ መንገድ ነው:: እንዲሁም ይህ የተገኘበት ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክሊገለጽ ይችላል:: አት “ከእኛ አንዱ ጽዋውን/ዋንጫውን የሠረቀ ከተገኘ” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገለላለጽና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እኛ ደግሞ የጌታችን ባሮች እንሁን

እዚህ ጌታችን የቤቱን አዛዥ ያመለክታል ይህ በሁለተኛ ሰው መልክ ሲገለጽ ይችላል አት እንደባሪዎች ሊትወስደን ትችላለህ (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ሰው አገለላለጽ ይመልከቱ)

አሁን እንዲሁ እንደነገራችሁ ይሁን

መልካም ነው: እንዳላችሁት አደርጋለሁ:: እዚህ “አሁን” “በዚህ ጊዜ” ማለት አይደለም ነገር ግን የሚቀጥለው ዋና ነጥብ ትኩረትን ለመሳብ ተጠቅሞአል::

ጽዋው የተገኘበት ባሪያዬ ይሆናል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት ከስልቾቻችን በአንዱ ጽዋውን ካገኘው ያ የተገኘበት ሰው ባሪያዬ ይሆናል (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 44:11

የየራሱን ስልቻ ወደ ምድር አወረደ

የየራሱን ስልቻ አራገፌ

ከታላቁ … እስከታናሹ

“ወንድም” የተባለው ቃል የታወቀ ነው:: “ከታላቅ ወንድም ….እስከ ታናሽ ወንድም” (የተደበቁ ቃላትን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ጽዋው በታናሹ በብንያም ስልቻ ተገኘ

ይህ እንደ አድስ ዐረፍተ ነገርና ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል በታናሹ ወንድም የቤቱ አዛዥ ጽዋውን በብንያምን ስልቻ አገኘ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በዚህን ጊዜ እነርሱ ልብሳቸውን ቀደዱ

እዚህ እነርሱ ወንድምቹን ያመለክታል ልብስን መቅደድ የታላቅ ሐዘን ወይም ተካዜ ምልክት ነው (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

በየአህዮቻቸው…ተመለሱ

በየአህዮቻቸው…. እናም ተመለሱ

Genesis 44:14

እርሱ ገና እዚያው ነበረ

ዮሴፍ እዚያው ነበረ

በፊቱም መሬት ላይ ተደፉ

በፊቱም መሬት ላይ ወደቁ:: ይህ ወንድምቹ ጌታው ምሕረት እንዲያደርግላቸው የመፈለጋቸው ምልክት ነው:: (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

እንደ እኔ ያለ ሰው ምሥጢርን እንዲያውቅ አታውቁምን

ዮሴፍ ወንድሞቹን ለመቆጣት ጥያቄ ይጠቀማል:: አት “እንደ እኔ ያለ ሰው ስውር ነገርን በጥበብ እንደሚያውቅ ታውቃላችሁ” (ሽንገላን ያዘለ ጥያቄ ይመልከቱ)

Genesis 44:16

ለጌታዬ ምን እንመልሳለን? ምንስ እንናገራለን? ወይም በመን እንነጻለን?

ሶስቱም ጥያቄዎች ሁሉ ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: የተደረገውን ለመግለጽ የሚናገሩት ምንም እንደሌለ ትኩረት ለመስጠት እነዚህን ጥያቄዎች ይጠቀማሉ፡፡ አት “ጌታዬ የምንናገረው የለንም የሚረባ ነገር መናገር አንችልም ራሳችንን ንጹህ ማድረግ አንችልም” (ተመሣሣይ ተጓዳኝ አገላለጽ እና ሽንገላ አዘል ጥያቄዎች ይመልከቱ)

ለጌታዬ ምን እንላለን …. የጌታዬ ባሪያዎች

እዚህ ጌታዬ ዮሴፍን ያመለክታል ይህ ለአንድ ከፍተኛ ባለሥልጣን የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው በሁለተኛ ወገን ሰው መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ምን አንላለን … ባሪያዎችህ” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

እግዚአብሔር የአገልጋዮችን/የባሪያችህን በደል ገልጦአል

ወንድሞቹ ራሳቸውን እንደ ባሪያዎች ያቀርባሉ :: እዚህ ገለጠ የሚለው እግዚአብሔር ወንድሞቹ ያደረጉትን ገለጠ ማለት አይደለም:: ነገር ግን እነርሱ ስላደረጉት ነገር እግዚአብሔር እየቀጣቸው ነው የሚል ትርጉም አለው:: አት “እግዚአብሔር ላለፈው ኃጢአት እየቀጣቸው ነው”

የባሪያዎችህን በደል

ወንድሞቹ ራሳቸውን እንደ ባሪያዎች ያቀርባሉ:; ይህ ለአንድ ከፍተኛ ባለሥልጣን የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው:: በአንደኛ ወገን ሰው መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “በደላችንን” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

እንግዲህ ጽዋው በእጁ የተገኘበት

እዚህ “እጅ” ሙሉ ሰው ይወክላል:: እንዲሁም የተገኘበት የሚለው ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:; አት “ጽዋህን የወሰደው” (ምትክ ቃል አጠቃቀምና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ይህን ማድረግ ከእኔ ይራቅ

አንድ ሰው የማያደርገው አንድ ነገር ያ ሰው ከራሱ አርቆ የሚያቀምጠው ዕቃ ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “ያን ነገር የሚያደርግ የእኔ ዓይነት አይደለም” (ዘይቤያዊ አነጋYገር ይመልከቱ)

ጽዋው በእጁ የተገኘበት ሰው

እዚህ “እጅ” ሙሉ ሰው ይወክላል:: እንዲሁም የተገኘበት የሚለው ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:; አት “ጽዋዬን የወሰደው ሰው” (ምትክ ቃል አጠቃቀምና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Genesis 44:18

ቀረብ ብሎ

ተጠግቶ

እኔ አገልጋይህ

ይሁዳ ራሱን እንደ “አገልጋይህ ወይም ባሪያህ” ያመለክታል:: ይህ ለአንድ ከፍተኛ ባለሥልጣን የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው:: ይህ በአንደኛ ወገን ሰው መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እኔ ባሪያህ ወይም አገልጋይህ”(አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

በጌታዬ ጆሮ አንዲት ቃል እንድናገር

“ጆሮ” የሚለው ለሙሉ ሰው የሚሆን ምትክ ቃል ነው፡፡ አት “ጌታዬ ሊናገርህ” (ምትክ ቃል አጠቃቀም ይመልከቱ)

በጌታዬ ጆሮ

እዚህ ጌታዬ ዮሴፍን ያመለክታል፡፡ ይህ ለአንድ ከፍተኛ ባለሥልጣን የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው:: ይህ በሁለተኛ ወገን ሰው መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ለአንተ”(አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

እኔን አገልጋይህን ቁጣህ አያቃጥለኝ

መቆጣት እንደሚያቃጥል እሳት ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “አባክህን እኔን አገልጋይህን አትቆጣኝ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አንተ እንደፈርዖን ነህና

ጌታው ትልቅ ሥልጣን እንዳለው ትኩረት ለመስጠት ከፈርዖን ጋር ያወዳድረዋል:: ይህም የሚገልጸው ሊቆጣውም ሊገድለውም እንደሚችል ነው አት “እንደ ፈርዖን ኃይለኛ ስለሆንህና ወታደሮችህም ሊገድሉኝ ስለሚችሉ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቀ መረጃ ይመልከቱ)

ጌታዬ ባሪያዎቹን፤ “አባት አላችሁ ወይም ወንድም?”ብሎ ጠየቀ::

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ የያዘ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ጌታዬ አባት ወይም ወንድም እንዳለን ጠየቀን” (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ጌታዬ ባሪያዎቹን ጠየቀ

ይሁዳ ዮሴፍን “ጌታዬ” እና “እርሱ” በሚሉ ቃላት ያመለክተዋል:: አንዲሁም ደግሞ ወንድሞቹንና ራሱን እንደ “የእርሱ ባሪያዎች” ይገልጻል:: አት “አንተ ጌታዬ ባሪያዎችህን ጠየቅሄን ወይም አንተ ጠቀየቅሄን” (አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን አገላለጽ ይመልከቱ)

Genesis 44:20

አጠቃላይ መረጃ

በዮሴፍ ፊት መናገሩን ይሁዳ ቀጠለ

እኛም ለጌታዬ እንዲህ አልን ‘ሽማግሌ አባት አለን …. አባቱም ይወድደዋል’

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ የያዘ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እናም እኛ እንዲህ አልን ‘አባት አለን አባቱም ይወድደዋል’” (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ለጌታዬ እንዲህ አልን

ይሁዳ ዮሴፍን እንደ “ጌታዬ” ያመለክተዋል:: ይህ ለአንድ ከፍተኛ ባለሥልጣን የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው:: አት “ጌታዬ እኛም እንዲህ አልን”(አንደኛ ሁለተኛና ሶስተኛ ወገን አገላለጽ ይመልከቱ)

አባቱም ይወድደዋል

ይህ ለጓደኛ ወዳጅ ወይም ለቤተሰብ አባል ያለውን ፍቅር ይገልጻል

ከዚያም ለባሪያዎችህ ወደእኔ አምጡት እኔም አየዋለሁ እልህ

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ የያዘ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እናም አንተ ለባሪያዎችህን ታናሽ ወንድማችሁን አምጡት እኔም አየዋለሁ አልህ’” (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ከዚያም ለባሪያዎችህ እንዲህ አልህ

ይሁዳ ወንድሞቹንና ራሱን እንደ እርሱ ባሪያዎች ያመለክታል:: አት “ከዚያም ለእኛ ለባሪያዎችህ እንዲህ አልህ”(አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን አገላለጽ ይመልከቱ)

ወደ እኔ ይዛችሁ ውረዱ

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ ሲነገር መውረድ የሚለው ቃል የተለመደ ነው:: አት “ወደ እኔ አምጡት” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ከዚያም በኋላ ጌታዬን አልነው “ብላቴናው… አይሆንለትም …አባቱ ይሞታልና”

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ የያዘ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “መልሰን እኛም ለጌታዬ ልጁ ….አይችልም፤ ….አባትየው ይሞታል” (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

አባትዬው ይሞታል

ከማዘን የተነሣ አባታቸው እንደሚሞት ይገልጻል (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 44:23

አጠቃላይ መረጃ

ይሁዳ ታሪኩን ለዮሴፍ መናገር ቀጠለ

ከዚያም ባሪያዎችህን እንዲህ አልሄን፤ ታናሽ ወንድማችሁ ከእናንተ ጋር ጋር ካልመጣ ዳግመኛ ፊቴን አታዩም

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ የያዘ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ከዚያም ለባሪያዎችህ ታናሽ ወንድማችን ከእኛ ጋር ካልመጣ ፊቴን አታዩም አልሄን ” (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ከዚያም ለባሪያዎችህ አልህ

ይሁዳ ራሱንና ወንድሞቹን እንደ “እርሱ ባሪያዎች” ያመለክታል፡፡ ይህ ትልቅ ባለሥልጣን ለሆነ ለአንድ ሰው የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው፡፡ (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን አገላለጽ ይመልከቱ)

ይዞ መውረድ …ወደ ታች መውረድ

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ ሲነገር መውረድ የሚለው ቃል የተለመደ ነው::

ዳግመኛ ፊቴን አታዩም

እዚህ “ፊት” ሙሉ ሰውን ይወክላል:: አት እንደገና አታዩኝም (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

ከዚያም እንዲህ ሆነ

ይህ ሀረግ የተጠቀመው የታሪኩ አድስ ክፍል መጀመሩን ለማመለከት ነው:: በቋንቋዎ ይህን የሚገልጹበት መንገድ ካለ ይጠቀሙ:: (አድስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

ወደ ባሪያህ ወደ አባታችን በወጣን ጊዜ

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ ሲነገር “ወደ ላይ መውጣት” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነው

የጌታዬን ቃል ነገርነው

ይሁዳ ዮሴፍን እንደ “ጌታዬ” ያመለክታል:: አት ጌታዬ የነገርከውን ቃል ነገርነው”(አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን አገላለጽ ይመልከቱ)

አባታችን ‘ተመልሳችሁ ጥቂት እህል ሸምቱልን አለ’

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ የያዘ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “አባታችን አንደገና ወደ ግብጽ በመሄድ ለእኛና ለቤተሰቦቻችን እህል እንድንሸምት ተናገረን ” (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

እኛም አልነው ‘መሄድ አንችልም ታናሽ ወንድማችን ከእኛ ጋር…’

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ የያዘ ነው እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ከዚያም ለእርሱ ወደ ግብጽ መውረድ አንችልም አልን ታናሽ ወንድማችን ከእኛ ጋር … ከእኛ ጋር ” (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

የሰውየውን ፊት ማየት

እዚህ ፊት ሙሉ ሰውን ይወክላል:: አት “ሰውየውን ለማየት” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

Genesis 44:27

ይሁዳ ታሪኩን ለዮሴፍ መናገርን ቀጠለ

እንዲህ አለን ሚስቴ ሁለት ወንዶች ልጆችን እንደወለደችልን እናንተ ታውቃላችሁ አንዱ ከእኔ ወጣ አውሬ በላው አላችሁኝ እስከ ዛሬም አላየሁትም ይህንም ከእኔ ለይታችሁ ደግሞ ብትወስዱ ክፉም ቢያገኘው ሽበቴን በሐዘን ወደ መቃበር ታወርዱታላችሁ ይህ ሁለት ደረጃና ሶስት ደረጃ ጥቅሶችን ይዞአል እነዚህም እንደተዘዋዋሪ ጥቅሶች ሊገለጹ ይችላሉ አት እንዲህ አለን ሚስቱ ራሔል ሁለት ወንዶች ልጆችን ብቻ እንደወለደችለት እናውቃለን ከእነርሱ አንዱ ወጣና አውሬ በላው እናም እስከ ዛሬ አላየሁትም ሌላውን ልጅ ብንወስደውና ክፉ ቢያገኘው በሐዘን እንዲሞት እናደርጋለን (ጥቅስን በጥቅስ ውሰጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)ከዚይ አለ

እኛን እንዲህ አለን

እዚህ “እኛ” ዮሴፍን አያካትትም (ነጠላና ብዙ ወይም አካታች “እኛ” ይመልከቱ)

እናንተ ታውቃላችሁ

እዚህ “እናንተ” ብዙና ወንድሞቹን ያመለክታል (“እናንተ” አጠቃቀም ዓይነት ይመልከቱ)

በእውሬ ተበላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት አውሬ በላው ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ

ጉዳት ቢደርስበት

ለአንድ ሰው አንድ ክፉ ነገር የሚደርሰበት ጉዳት ወደዚያ ሰው እንደሚመጣ ተደርጐ ተቆጥሮአል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሽበተን በሐዘን ወደ መቃብር ታወርዱታላችሁ

“ወደ መቃብር ማውረድ” እንዲሞትና ወደ መቃብር እንዲወርድ ማድረግ ማለት ነው:: “ማውረድ” የሚለውን ቃል የተጠቀመው መቃብር በመሬት ውስጥ እንደሆነ በተለምዶ የታወቀ ስለሆነ ነው:: አት “ከዚያም እኔን ሽማግሌውን በሐዘን እንዲሞት ታደርጋላችሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሽበቴን

ያዕቆብን የሚያመለክትና ሽምግልናውን አበክሮ የሚናገር ነው:: አት “እኔ ሽማግለው” (ምትክ ቃል አጠቃቀም ይመልከቱ)

Genesis 44:30

አሁን

ይህ በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም ነገር ግን ለሚቀጥለው ጠቃሚ ነገር ትኩረት እንዲሰጥበት ተጠቅሞአል

እንግዲህ በምንመለስበት ጊዜ … በሐዘን ወደ መቃብር

ይሁዳ ያለ ብንያምን ወደ አባቱ በሚመለስበት ጊዜ ምን ሊፈጠር እንደሚችል የሚገምተውን ነገር ግን እውነት የሆነውን ለዮሴፍ ይገልጻል (ግምታዊ ሁኔታዎችን ይመልከቱ)

ወደ ባሪያህ በሚመጣበት ጊዜ

እዚህ “መምጣት” “መሄድ” ወይም “መመለስ” በሚለው መተርጐም ይችላል::

ብላቴናው ከእኛ ጋር አለመኖር

ልጁ ከእኛ ጋር አለመኖር

ሕይወቱ ከልጁ ሕይወት ጋር የተሣሠረ ስለሆነ

አባታቸው ልጁ ከሞቴ እሞታለሁ ያለው አባባል የሁለቱ ሕይወት በአካል በጥብቅ የተሣሠረ እንደሆነ ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “እርሱም ልጁ ካልተመለሰ እሞታለሁ ስላለ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እንዲህም ሆነ

ይሁዳ ወደፊት ይሆናል ብሎ ስለሚገምተው ነገር በእርግጥ እደሚደረግ አድርጐ ይናገራል (ግምታዊ ሁኔታዎች ይመልከቱ)

ባሪያዎችህ የባሪያህን የአባታችንን ሽበት በሐዘን ወደ መቃብር ያወርዳሉ

ወደ መቃብር ማውረድ እንዲሞትና ወደ መቃብር እንዲወርድ ማድረግ ማለት ነው:: “ማውረድ” የሚለውን ቃል የተጠቀመው መቃብር በመሬት ውስጥ እንደሆነ በተለምዶ የታወቀ ስለሆነ ነው:: አት “እናም ሽማግሌውን አባታችንን በሐዘን እንዲሞት እናደርጋለን” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ባሪያዎችህ ወይም አገልጋዮችህ

ይሁዳ ራሱንና ወንድሞችን “ባሪያዎችህ” ብሎ ያመለክታል:: ይህ ለአንድ ትልቅ ባለሥልጣን መደበኛ መንገድ የሚነገርለት ነው:: አት “እኛ አገልጋዮችህ” ወይም “እናም እኛ” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገንነ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

የባሪያህን የአባታችንን ሽበት

እዚህ “ሽበት” ያዕቆብን የሚወክልና ሽምግልናውን የሚናገር ነው:: አት “ሽማግሌው አባታችን” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ) ስለ ልጁ ደኀንነት በአባቴ ፊት ራሴን ዋስ አድርጌአለሁ ረቂቅ ስም ዋስ ተስፋ በሚለው ግሥ ሊገለጽ ይችላል አት ልጁን በሚመለከት ለአባቴ ተስፋ ስጥቼዋለሁ ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ

ባሪያህ

ይሁዳ ራሱን “ባሪያህ” ብሎ ያመለክታል፡፡ አት “ለእኔ ለባሪያህ” ወይም “ለእኔ” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

በአባቴ ፊት በደሌን እሸከማለሁ

እንደበደለኛ መቆጠር በደል እንድሰው የሚሸከመው ነገር ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “አባቴ ይወቅሰኛል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 44:33

አሁን

ይህ በአሁን ጊዜ ማለት አይደለም ነገር ግን ለሚቀጥለው ዋና ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ተጠቅሞአል::

ባሪያህ

ይሁዳ ራሱን “ባሪያህ” ብሎ ያመለክታል፡፡ አት “እኔ ለባሪያህ” ወይም “እኔ” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ልጁ… ይውጣ

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ መውጣት የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነበር

ልጁን ሳልይዝ እንዴት ተመልሼ ወደ አባቴ እሄዳለሁ?

ብንያምን ወደ ቤት ካልተመለሰ አባቱ ሊኖረው የሚችለውን ሐዘን ለማተኮር ይሁዳ ጥያቄ ይጠቀማል:: አት “ልጁ ከእኔ ጋር ካልሆነ ወደ አባቴ መመለስ እልችልም“ (አግናኝ ወይም ሽንገላ አዘል ጥያቄዎች ይመልከቱ)

በአባቶ ላይ የሚደርሰውን መከራ እንዳላይ

ከባድ መከራ የደረሰበት ሰው በዚያው ሰው ክፉ ነገር እንደመጣበት ተደርጐ ተነግሮአል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)


Chapter 45

1 በዚያን ጊዜ ዮሴፍ አጠገቡ በነበሩ ሰዎች ፊት ስሜቱን ሊገታ ባለመቻሉ፣ “እዚህ ያሉትን ሰዎች በሙሉ አስወጡልኝ” ብሎ ጮኾ ተናገረ፤ ስለዚህም ዮሴፍ ራሱን ለወንድሞቹ በገለጠበት ጊዜ ከእርሱ ጋር ሌላ ማንም ሰው አልነበረም። 2 ዮሴፍም ድምፁን ከፍ አድርጎ በማልቀሱ ግብፃውያን ሰሙት፣ ወሬውም ወደ ፈርዖን ቤተ ሰዎች ደረሰ። 3 ዮሴፍም ወንድሞቹን፣ “እኔ ዮሴፍ ነኝ፤ ለመሆኑ አባቴ እስካሁን በሕይወት አለ?” ሲል ጠየቃቸው። ወንድሞቹ ግን በፊቱ ተደናግጠው ስለነበር መልስ ሊሰጡት አልቻሉም። 4 ዮሴፍም ወንድሞቹን፣ “እስቲ ወደ እኔ ቀረብ በሉ” አላቸው፣ ወደ እርሱም በቀረቡ ጊዜ እንዲህ አለ፤ “ወደ ግብፅ የሸጣችሁኝ እኔ ዮሴፍ ነኝ፤ 5 አሁንም በመሸጣችሁ አትቆጩ፤ በራሳችሁም አትዘኑ፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ሕይወት ለማዳን ሲል ከእናንተ አስቀድሞ እኔን ወደዚህ ልኮኛል። 6 በምድር ላይ ራብ ከገባ ይኸው ሁለት ዓመት ሆነ፣ ከዚህ በኋላም የማይታረስባቸውና ሰብል የማይሰበሰብባቸው አምስት ዓመታት ገና አሉ። 7 ነገር ግን እግዚአብሔር ሕይወታችሁን በታላቅ ማዳን ለመታደግና ዘራችሁ ከምድር ላይ እንዳይጠፋ በማሰብ ከእናንተ አስቀድሞ ወደዚህ ላከኝ። 8 ስለዚህ አሁን ወደዚህ የላከኝ እግዚአብሔር እንጂ እናንተ አይደላችሁም፣ እርሱም ለፈርዖን እንደ አባት፤ በቤት ንብረቱ ላይ ጌታ፣ እንዲሁም በግብፅ ምድር ላይ ገዢ አደረገኝ። 9 አሁንም ‘በፍጥነት ወደ አባቴ ተመልሳችሁ እንዲህ በሉት፤ “ልጅህ ዮሴፍ እንዲህ ይላል፤ ‘እግዚአብሔር የመላው ግብፅ ጌታ አድርጎኛል፤ ስለዚህ ሳትዘገይ ወደ እኔ ና። 10 ልጆችህን የልጅ ልጆችህን በጎችህን፣ ፍየሎችህን ከብቶችህንና ያለህን ሁሉ ይዘህ በአቅራቢያዬ በጌሤም ትኖራለህ። 11 ገና ወደ ፊት የሚመጣ የአምስት ዓመት ራብ ስላለ፣ በዚያ የሚያስፈልጋችሁን እኔ እሰጣችኋለሁ፤ ያለበልዚያ ግን አንተና ቤተ ስዎችህ ያንተም የሆነው ሁሉ፣ ችግር ላይ ትወድቃላችሁ።’ 12 ፊታችሁ ሆኜ የማናግራችሁ እኔ ዮሴፍ ራሴ መሆኔን እናንተም ሆናችሁ ወንድሜ ብንያም በዓይናችሁ የምታዩት ነው። 13 በግብፅ ስላሏኝ ክብርና ስላያችሁትም ሁሉ ለአባቴ ንገሩት፣ አባቴንም በፍጥነት ይዛችሁት ኑ። 14 ከዚያም በወንድሙ በብንያም አንገት ላይ ተጠምጥሞ አለቀሰ፤ ብንያምም እያለቀሰ ዮሴፍን አቀፈው። 15 የቀሩትምንም ወንድሞቹን አንድ በአንድ እየሳመ አለቀሰ። ከዚያም ወንድሞቹ ከእርሱ ጋር መጨዋወት ጀመሩ። 16 የዮሴፍ ወንድሞች መምጣት በፈርዖን ቤተ መንግሥት በተሰማ ጊዜ፣ ፈርዖንና ሹማምንቱ ሁሉ ደስ አላቸው። 17 ፈርዖን ዮሴፍን እንዲህ አለው፤ “ለወድሞችህ እንዲህ ብለህ ንገራቸው፣ ‘እንዲህ አድርጉ እህዮቻችሁን ጭናችሁ ወደ ከነዓን ምድር ተመለሱ። 18 ከዚያም አባታችሁንና ቤተ ሰባችሁን ይዛችሁ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም እጅግ ለም ከሆነው የግብፅ ምድር እሰጣችኋለሁ፤ በምድሪቱ በረከት ደስ ብሎአችሁ ትኖራላችሁ።’ 19 ደግሞም እንዲህ ብለህ እዘዛቸው፤ ‘ይህን አድርጉ፣ ከግብፅ ምድር ልጆቻችሁንና ሚስቶቻችሁን የምታጓጉዙባቸው ሠረገላዎች ወስዳችሁ፤ አባታችሁን ይዛችሁ ኑ። 20 ስለ ንብረታችሁ ምንም አታስቡ፣ ከግብፅ ምድር እጅግ ለም የሆነው የእናንተ ይሆናልና።’” 21 የእስራኤልም ልጆች ይህንኑ አደረጉ። ዮሴፍም ፈርዖን ባዘዘው መሠረት ሠረገላዎች አቀረበላቸው፤ የመንገድም ስንቅ አስያዛቸው። 22 ለእያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት የክት ልብስ ሰጣቸው፤ ለብንያም ግን ሶስት መቶ ጥሬ ብርና አምስት የክት ልብስ ሰጠው። 23 ለአባቱም በግብፅ ምድር ከሚገኘው የተመረጠ ነገር በዐሥር አህዮች፣ እንደዚሁም በዐሥር እንስት አህዮች ዳቦና ሌላ ምግብ አስጭኖ ሰደደለት። 24 ከዚህ በኋላ ወንድሞቹን አሰናበታቸው፤ ከእርሱም ሲሰናበቱ፣ መንገድ ላይ እንዳትጣሉ” አላቸው። 25 እነርሱም ከግብፅ ወጥረው በከነዓን ምድር ወደሚኖረው ወደ አባታቸው ወደ ያዕቆብ መጡ። 26 አባታቸውንም፣ እነሆ ዮሴፍ በሕይወት አለ፤ እንዲያውም በግብፅ ምድር ሁሉ ገዥ ሆኖአል” ብለው ነገሩት። ያዕቆብ ግን እጅግ ደነገጠ፤ ሊያምናቸውም አልቻለም። 27 ነገር ግን ዮሴፍ ያላቸውን ሁሉ በነገሩት ጊዜና እርሱን ወደ ግብፅ የሚወስዱበትን ዮሴፍ የላከለትን ሠረገላ ባየ ጊዜ የአባታቸው የያዕቆብ መንፈስ ታደሰ። 28 ከዚያም እስራኤል፣ “ልጄ ዮሴፍ በሕይወት አለ፤ ከመሞቴ በፊት ሄጄ ዐየዋለሁ” አለ።



Genesis 45:1

ራሱን ሊቆጣጠር አልቻለም

ስሜቱን ሊገታ አልቻለም ማለት ነው ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ማልቀስ ጀምሮ ነበር”

ከጐኑ

አጠገቡ

የፈርዖን ቤት

እዚህ “ቤት” በፈርዖን ቤተመንሥት ያሉ ሰዎችን ይወክላል፡፡ አት “በፈርዖን በተመንግሥት ያለው ሁሉ” (ምትክ ቃላት የመጠቀም ዘይቤ ይመልከቱ)

በፊቱ ተደናግጠው

እርሱን ፈርተው

Genesis 45:4

ወደ ግብጽ የሸጣችሁኝ

ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ አት “ወደ ግብጽ ላመጡኝ ነጋዴዎች እንደ ባሪያ የሸጣችሁኝ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አትዘኑ

“አትቈጩ” ወይመ “አትጨነቁ”

ወደዚህ ስለሸጣችሁኝ

ትርጉሙም በግልጽ ሊነገር ይችላል፡፡ አት “እንደ ባሪያ ሸጣችሁኝ እናም ወደ ግብጽ ምድር ላካችሁን”

ሕይወት ለማዳን

እዚህ “ሕይወት” ዮሴፍ በረሃቡ ጊዜ ያዳናቸውን ሰዎች ይወክላል:: አት “የብዙ ሰዎችን ሕይወት እንዳድን” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

የማይታረስባቸውና ሰብል የማይሰበሰብባቸው አምስት ዓመታት ገና አሉ

የማይታረስባቸው ወይም ሰብል የማይሰበሰባቸው አምስት ዓመታት አሉ እዚህ የማይታረስባቸውና ሰብል የማይሰበስብባቸው ሰብሎች ከድርቁ የተነሣ እንደማይመረቱ የሚገልጹ ናቸው:: አት “ረሃቡ ለተጨማሪ አምስት ዓመታት ይቀጥላል” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

Genesis 45:7

በምድር ላይ ቅሬታን አስቀርላችሁ ዘንድ

“እናንተና ቤተሰቦቻችሁ ከምድር ላይ ፈጽማችሁ እንዳትጠፉ” ወይም “ዘራች ከምድር ላይ እንዲኖር”

ሕይወታችሁን በታላቅ ማዳን ለመታደግ

ማዳን የተባለው ረቂቅ ስም ማትረፍ በሚለው ሊገለጽ ይችላል:: አት “በታላቅ መንገድ በማትረፍ በሕይወት እንዲትኖሩ” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

ፈርዖን አባት አድርጐኛል

ዮሴፍ ፍርዖንን ማማከሩና መርዳቱ ዮሴፍ እንደፈርዖን አባት ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “የፈርዖን መሪ ወይም አማካሪ አድርጐኛል” ወይም “የፈርዖን ዋና አማካሪ አድርጐኛል” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

በቤቱ ሁሉ ላይ

እዚህ “ቤት” በቤተመንግሥቱ የሚኖሩ ሰዎችን ይወክላል:: አት “በቤተሰዎቹ ሁሉ ላይ” ወይም “በቤተመግሥቱ ላይ” (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

በግብጽ ምድር ሁሉ ላይ ገዥ

እዚህ “ምድር” ሰዎችን ይወክላል:: አት “በግብጽ ምድር ሰዎች ሁሉ ላይ ገዥ” (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

ገዥ

ዮሴፍ ከግብጽ ንጉሥ ፈርዖን ሁለተኛ ደረጃ ገዥ ነው ማለት ነው:: ይህ የተነገረው መረጃ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 45:9

ወደ አባቴ ውጡ

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ ሲነገር ወደ ላይ መውጣት የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነበር:: አት “ወደ አባቴ ሂዱ”

እንዲህም በሉት ልጅህ ዮሴፍ እዲህ ይላል “እግዚአብሔር … ያለህን ሁሉ”

ይህ ሶስት ደረጃ ያለው ጥቅስ ነው በሁለት ደረጃዎች ቀለል ባለ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እኔ የምለውን ንገሩት እግዚአብሔር ያለህን ሁሉ” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ወደ እኔ ና/ውረድ

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ ሲነገር ወደ ታች መውረድ የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነበር:: አት “ወደዚህ ወደ እኔ ና”

ወደ ችግር ና

ችግርን እንደ መድረሻ አድርጐ ይናገራል:: አት “ማጣት” ወይም “ረሀብ” (ዘይቤያዊ አነገር ይመልከቱ)

Genesis 45:12

የእናንተ ዐይኖች አይተዋል እናም የወንድማችሁ የብንያምም ዐይኖች አይተዋል

እዚህ “ዐይኖች” ሙሉ ሰው ይወክላሉ:: አት “እናንተ ሁላችሁና ብንያም ታያላችሁ” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ለእናንተ የተናገረቻችሁ የእኔ አፍ እንደሆነች

እዚህ አፍ ሙሉ ሰውን ይወክላል፡፡ አት “እኔ ዮሴፍ እነግራችኋለሁ” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በግብጽ ስላለኝ ክብር ሁሉ

የግብጽ ሰዎች በታላቅነት እንዴት እንደሚያከብሩኝ

አባቴን ወደ ታች ወደዚህ አምጡት

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ ሲነገር ወደ ታች መውረድ የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነበር:: አት “አባቴን ወደዚህ አምጡት”

Genesis 45:14

የወንድሙን የብንያምንም አንገት አቀፎ አለቀሰ ብንያምም በአንገቱ ላይ አለቀሰ

ዮሴፍ ወንድሙን ብንያምን አቀፈውና ሁለቱም አለቀሱ

ወንድሞቹን ሁሉ ሳማቸው

በጥንታዊቷ ቅርብ ምሥራቅ ዘመድን በመሳም ሰላምታ መስጠት የተለመደ ነበር:: በቋንቋዎ እንዲህ የመሰለ ስሜት ገላጭ ሰላምታ አሰጣጥ ካለ ያን ይጠቀሙ:: ከሌለ ግን ተገቢ የሆነውነ ቃል ይጠቀሙ::

እየሳማቸው አለቀሰ

ይህም ዮሴፍ በሳማቸው ጊዜ እያለቀሰ ነበር ማለት ነው

ከዚያም በኋላ ወንድሞቹ ከእርሱ ጋር መነጋገር ጀመሩ

አስቀድመው ሊነጋገሩ ፈርተው ነበር:: አሁን ግን በነጻነት መነጋገር እንደሚችሉ ተሰማቸው:: የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉሙ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “ከዚያም በኋላ ወንድሞቹ ከእርሱ ጋር በነጻነት መነጋገር ጀመሩ” (ግምታም እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 45:16

በፈርዖን ቤት የዮሴፍ ወንድሞች መጡ ተብሎ ወሬ ተሰማ

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ ይዞአል:: እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊጠቀስ ይችላል:: እንዲሁም ደግሞ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “የዮሴፍ ወንድሞች እንደመጡ በፈርዖን ቤተመንግሥት ያለው ማንኛውም ሰው ሰማ” (ጥቅስን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅስ እናም ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የፈርዖን ቤት

የፈርዖንን ቤተመንሥት ይወክላል

ለወንድሞችህ እንዲህ ብለህ ንገራቸው፤ ይህን አድርጉ አህዮቻችሁን ጭናችሁ ወደ ከነዓን ምድር ሂዱ፤ አባታችሁንና ቤተሰባችሁን ይዛችሁ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም እጅግ ለም ከሆነው የግብጽ ምድር እሰጣችኋለሁ፤ የምድርቱንም ስብ/በረከት ትበላላችሁ፡፡

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ ይዞአል:: እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊጠቀስ ይችላል:: አት “አህዮቻቸውን እንዲጭኑና ወደ አባታቸውና ቤተሰቦቻውው ወደ ከነዓን እንዲሄዱ ለወንድሞችህ ንገራቸው፤ ወደዚህ እንዲመጡና እኔም እጅግ ለም ከሆነው የግብጽ ምድር እንደሚጣቸወ፤ የምንሰጠውን በረከት እንደሚመገቡ ደግሞም ንገራቸው” (ጥቅስን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅስ ይመልከቱ)

እኔም መልካም ከሆነው የግብጽ ምድር እሰጣችኋለሁ፤

እኔም እጅግ ለም የሆነውን የግብጽ ምድር እሰጣችኋለሁ

የምድርቱንም ስብ ትበላላችሁ

ምድርቱ የሚትሰጠው መልካም እህል እንደ ምድሪቱ ስብ ተደርጐ ተቆጥሮአል:: አት “የምድሪቱንም እህል ትመገባላችሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 45:19

አጠቃላይ መረጃ

ዮሴፍ ለወንድሞቹ ምን መናገር እንዳለበት ፈርዖን መናገሩን ቀጠለ

አሁን

ይህ በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም ነገር ግን ለሚቀጥለው ጠቃሚ ነጥብ/ ቁም ነገር ትኩረት እንዲሰጥበት ተጠቅሞአል

እንዲህ ብለህ እዘዛቸው ይህን አድርጉ ከግብጽ ምድር ልጆቸችሁንና ሚስቶቻችሁን የምታጓጉዙበት ሠረገላዎች ውሰዱ አባታችሁንም ይዛችሁ ኑ ስለንብረታችሁ ምንም አታስቡ ከግብጽ ምድር እጅግ ለም የሆነው የእናንተ ነውና

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ ይዞአል:: እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊጠቀስ ይችላል:: አት “ደግሞም ከግብጽ ምድር ልጆቸችሁንና ሚስቶቻችሁን እናም አባታችሁንም ይዘው እንዲመጡ የሚያጓጉዙበትን ሠረገላዎች እንዲወስዱ ንገራቸው እኔም በግብጽ መልካም የሆነውን ስለሚሰጣቸው ንብረታችሁን ይዘው ለመምጣት ምንም አይጨነቁ (ጥቅስን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅስ ይመልከቱ)

ታዝዘሃል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት “ደግሞም እንትነግራቸው አዝሃለሁ ወይም ደግሞም ንገራቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ሠረገላዎችን ይውሰዱ

ሠረገላዎች ሁለት ወይም አራት ጐማ ያላቸው የጭነት ሠረገላዎች ናቸው እንስሳት ተሳቢውን ይገትቱታል

Genesis 45:21

ለመንገድ ስንቅ ሰጣቸው

ለጉዞአቸው የሚያስፈልጋቸውን ሰጣቸው

ለሁሉም ሁለት ሁለት መለወጫ ልብስ ሰጣቸው

አምስት መለወጫ ልብስ ከተሰጠው ከብንያምን በስተቀር ሌሎች አያንዳንዳቸው ሁለት መለወጫ ልብስ ተቀብለዋል (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሶስት መቶ ጥሬ ብር

3ዐዐ ጥሬ ብር (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

አሥር እህዮች … አሥር እንስት አህዮች

አህዮቹ በሥጦታው ተካትተዋል (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 45:24

አትጣሉ

ተገቢ ትርጉሞች የሚያጠቃልሉት 1) አትከራከሩ 2) አትኮራረፉ

ከግብጽ ወጥተው ወደ ላይ ወጡ

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደላይ” የሚለው ቃለ መጠቀም የተለመደ ነው

በግብጽ ምድር ሁሉ ገዥ ሆኖአል

እዚህ “የግብጽ ምድር” የግብጽ ሰዎችን ይወክላል አት በግብጽ ሰዎች ሁሉ ላይ ገዥ ሆኖአል:: (ምትከ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

ልቡ ደነገጠ

እነርሱ የተናገሩትን እንደ እውነት መቀበል አቃተው

Genesis 45:27

ነገሩት

ለያዕቆብ ነገሩት

ዮሴፍ የነገራቸውን ነገር ሁሉ

ዮሴፍ የነገራቸውን ማንኛውንም ነገር

የአባታቸው የያዕቆብ መንፈስ ታደሰ

እዚህ መንፈስ ሙሉ ሰው ይወክላል፡፡ አት “አባታቸው ያዕቆብ ከጭንቀቱ/ከሐዘኑ ተሻለው” ወይም “አባታቸው ያዕቆብ እጅግ ደስተኛ ሆነ” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም የመልከቱ)


Chapter 46

1 እስራኤልም ጓዙን ሁሉ ጠቅልሎ ተነሣ፤ ቤርሳቤህም ሲደርስ፣ ለአባቱ ለይስሐቅ አምላክ መሥዋዕት ሠዋ። 2 እግዚአብሔርም ሌሊት በራእይ ለእስራኤል ተገልጦ፣ “ያዕቆብ፣ ያዕቆብ” ብሎ ጠራው። እርሱም፣ “እነሆ፣ አለሁ” አለ። 3 እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፤ “እኔ የአባትህ አምላክ እግዚአብሔር ነኝ፤ ወደ ግብፅ ለመውረድ አትፍራ፤ በዚያ ታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁና፤ 4 አብሬህ ወደ ግብፅ እወርዳለሁ፣ ከዚያም መልሼ አወጣሃለሁ፣ የዮሴፍ የራሱ እጆች በምትሞትበት ጊዜ ዓይኖችህን ይከድናል። 5 ከዚህ በኋላ ያዕቆብ ከቤርሳቤህ ተነሣ፤ የእስራኤል ወንዶች ልጆችም አባታቸውን ያዕቆብን ልጆቻቸውንና ሚስቶቻቸውን ፈርዖን ለያዕቆብ በላከላቸው ሠረገላ ላይ አወጧቸው። 6 ከብቶቻቸውንና በከነዓን ምድር ያፈሩትን ሀብት ንብረታቸውን ይዘው፣ ያዕቆብና ዘሮቹ በሙሉ ወደ ግብፅ ወረዱ። 7 ወደ ግብፅም የወረደው፤ ወንዶች ልጆቹንና ወንዶች የልጅ ልጆቹን፣ ሴቶች ልጆቹንና የልጅ ልጆቹን ማለት ዘሮቹን ሁሉ ይዞ ነው። 8 ወድ ግብፅ የወረዱት የእስራኤል ልጆች፣ የያዕቆብ ዘሮቹ እነዚህ ናቸው፦ የያዕቆብ የበኩል ልጆ ሮቤል። 9 የሮቤል ልጆች፦ ሄኖኅ፣ ፈሉሶ፣ አስሮን እና ከርሚ ናቸው። 10 የስሞዖን ልጆች፦ ይሙኤል፣ ያሚን፣ ኦሃድ፣ ያኪን፣ ጸሐርና ከከነዓናዊቷ ሴት የተወለደው ሳኡል ናቸው። 11 ልጆች፦ ጌድሶን፣ ቀዓትና ሜራሪ ናቸው። 12 የይሁዳ ልጆች፦ ዔር አውናን፣ ሴሎም፣ ፋሬስ እና ዛራ ናቸው። ነገር ግን ዔርና አውናን በከነዓን ምድር ሞቱ። 13 የይሳኮር ልጆች፦ ቶላ፣ ፉዋ፣ ዮብና ሺምሮን ናቸው፤ 14 የዛብሎን ልጆች፦ ሴሬድ፣ ኤሎንና ያሕልኤል ናቸው፤ 15 እነዚህ ወንዶች ልጆች ያዕቆብ በሰሜን ምዕራብ መሰጴጦምያ ሳለ፣ ልያ የወለደችለት ናቸው። ሴቷን ዲናን ጨምሮ፣ የወንዶችና የሴቶች ልጆቹ ቁጥር ሠላሳ ሦስት ነው። 16 የጋድ ልጆች፦ ጽፎን፣ ሐጊ፣ ሹኒ፣ ኤስቦን፣ ዔሪ፣ አሮዲና አርኤሊ ናቸው፤ 17 የአሴር ልጆች፦ ዩምና፣ የሱዋ፣ የሱዊና በሪዓ ናቸው፤ እኅታቸውም ሤራሕ ናት፤ የበሪዓ ልጆች፦ ሐቤርና መልኪኤል ናቸው፤ 18 እነዚህ ዐሥራ ስድስት ልጆች ሁሉ ላባ ለልጁ ለልያ ከሰጣት ከዘለፋ ላይ ያዕቆብ የወለዳቸው ናቸው። 19 የያዕቆብ ሚስት የራሔል ልጆች፦ ዮሴፍና ብንያም ናቸው፤ 20 በግብፅም የኦን ከተማ ካህን የጶጥፌራ ልጅ አስናት፣ ምናሴንና ኤፍሬምን ለዮሴፍ ወለደችለት። 21 የብንያም ልጆች፦ቤላ፣ ቤኬር፣ አስቤል፣ ጌራ፣ ንዕማን፥ አኪ፣ ሮስ፥ ማንፌን፣ ሑፊምና አርድ ናቸው። 22 እነዚህ ዐሥራ አራቱ፣ ራሔል ለያዕቆብ የወለደችለት ልጆችና የልጅ ልጆች ናቸው። 23 የዳን ልጅ፦ ሑሺም ነው፤ 24 የንፍታሌም ልጆች፦ ያሕጽኤል፣ ጉኒ፣ ዮጽርና ሺሌም ናቸው፤ 25 እነዚህ ሰባቱ ልጆች ሁሉ ላባ ለልጁ ለራሔል ከሰጣት ከባላ ላይ ያዕቆብ የወለዳቸው ናቸው። 26 ከያዕቆብ ጋር ወደ ግብፅ የሄዱት የገዛ ዘሮቹ ብዛት ስድሳ ስድስት ሲሆን የልጆቹን ሚስቶች አይጨምርም። 27 ዮሴፍ በግብፅ የወለዳቸውን ሁለት ልጆች ጨምሮ ወደ ግብፅ የወረደው የያዕቆብ ቤተ ሰብ ቁጥር ሰባ ነበር። 28 ያዕቆብም ወደ ጌሤም ለመሄድ መመሪያ ይቀበል ዘንድ፣ ይሁዳን አስቀድሞ ወደ ዮሴፍ ላከው። እርሱም ጌሤም ሲደርሱ፣ 29 ዮሴፍ ሠረገላውን አዘጋጅቶ፤ አባቱን እስራኤልን ለመቀበል ወደ ጌሤም አመራ። ዮሴፍ አባቱ ዘንድ እንደደረሰ አንገቱ ላይ ተጠምጥሞ ለረጅም ጊዜ አለቀሰ። 30 እስራኤልም ዮሴፍን፣ “በሕይወት መኖርህን ስላየሁ፣ ከእንግዲህ ብሞትም አይቆጨኝም” አለው። 31 ከዚህ በኋላ ዮሴፍ ወንድሞቹንና የአባቱን ቤተ ሰዎች እንዲህ አላቸው፤ “ወደ ፈርዖን ወጥቼ እነግረዋለሁ፤ እንዲህም እለዋለሁ፣ ‘በከነዓን ምድር የሚኖሩት ወንድሞቼና የአባቴ ቤተ ሰዎች ወደ እኔ መጥተዋል። 32 ሰዎቹ ከብት የሚጠብቁ ስለሆኑ እረኞች ናቸው፣ ሲመጡም በጎቻቸውን፣ ፍየሎቻቸውንና ከብቶቻቸውን እንዲሁም ያላቸውን ሁሉ ይዘው መጥተዋል። 33 ፈርዖን አስጠርቶአችሁ፣ ‘ሥራችሁ ምንድን ነው?’ ብሎ ቢጠይቃችሁ፤ 34 እናንተ፣ ‘እኛ አገልጋዮችህ ሥራችን ከልጅነታችን ጀምሮ ልክ እንደ አባቶቻችን ከብት ማርባት ነው’ ብላችሁ መልሱለት። ከብት አርቢዎች በግብፃውያን ዘንድ እንደ ጸያፍ ስለሚቆጠሩ፣ በጌሤም ምድር እንድትኖሩ ይፈቅድላችኋል።”



Genesis 46:1

ወደ ቤርሳቤህ ሄደ

ወደ ቤርባህ መጣ

እነሆ አለው

“አዎን እየሰማሁ ነኝ”

ወደ ግብጽ ለመውረድ

ከከነዓን ወደ ግብጽ መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደ ታች መውረድ” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነው::

ታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ

እዚህ አንተን የሚለው ነጠላ አገላለጽና ያዕቆብን የሚያመለክት ነው እዚህ ያዕቆብ ታላቅ የሚሆነውን የእርሱን ዘር ይወክላል አት ብዙ ትውልድ እሰጥሃለሁና እነርሱም ታላቅ ሕዝብ ይሆናሉ (አንተ የሚለውን ቃል አጠቃቀምና ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

ወደ ግብጽ ውስጥ

ወደ ግብጽ

ከዚያም ደግሞ እኔ አወጣሃለሁ

ተሰፋ የተሰጠው ለያዕቆብ ነው ነገር ግን ተስፋው የሚፈጸመው ለእስራኤል ትውልድ ሁሉ ነው አት በእርግጥ ዘርህን ከግብጽ ምድር አወጣለሁ (አንተ የሚለውን ቃል አጠቃቀምና ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

ደግሞም ወደ ላይ አወጣሃለሁ

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደላይ መውጣት” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነው::

የዮሴፍ የራሱ እጆች ዐይኖችህን ይገጥሟቸዋል

የራሱ እጆች ዐይኖችህን ይገጥሟቸዋል የሚለው ሀረግ እስራኤል በሚሞትበት ጊዜ ዮሴፍ እንደሚገኝና በሞቱ ጊዜ የዮሴፍ እጆች የያዕቆብን የዐይን ሽፋሽፍቶች እንደሚዘጉ የሚናገርበት መንገድ ነው:: አት “ዮሴፍም ቢሆን በሞትህ ዕለት ይገኛል” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ዐይኖችህን ይገጥሟቸዋል

አንድ ሰው ዐይኑን ከፍቶ በሚሞበት ጊዜ የዐይኑን ሽፋሽፍቶች መበሳብ መዝጋት የተለመደ ባህል ነበር:: የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 46:5

ተነሣ

ከዚያ ወጣ

በሠረገሎች

“ሠረገሎች” ሁለት ወይም አራት እግር ያላቸው የጭነት ሠረገሎች ናቸው እንስሳት ተሳቢውን ይጐትቱታል:: በዘፍትረት 45:19 ሠረገሎች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ያካበቱትን

“ያገኙትን” ወይም “ያፈሩትን”

ከራሱ ጋር ይዞ አመጣቸው

ያዕቆብ ከራሱ ጋር ይዞአቸው መጣ

የልጆቹን ወንድ ልጆች

ወንድ የልጅ ልጆች

የልጆቹን ሴት ልጆች

ሴት የልጅ ልጆች

Genesis 46:8

ስማቸው ይህ ነበር

ይህ ጸሐፊው የሚዘረዝራቸውን የሰዎች ስሞች ያመለክታል፡፡

የእስራኤል ልጆች

የእስራኤል ቤተሰብ አባላት ሄኖኀ ፌሉሶ አስሮንና ከርሚ…ይሙኤል ያሚን ኦሃድ ያኪን ጾሐርና ሳኡል …ጌድሶን ቀዓትና ሜራሪ፤ እነዚህ ሁሉ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 46:12

ዔር አውናን ሴሎም

እነዚህ ይሁዳ ከሚስቱ ከሰዋ የወለዳቸው ወንዶች ልጆች ነበሩ:: በዘፍጥረት 38:3-5 እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ፋሬስና ዛራ

እነዚህ ይሁዳ ከምራቱ ከታማር የወለዳቸው ወንዶች ልጆች ነበሩ:: በዘፍጥረት 38:29-30 እነዚህን ስሞች እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ኤስሮም ሐሙል … ቶላ ፋዋ ዮብ … ሺምሮን… ሴሬድ ኤሎን… ያሕልኤል

እነዚህ ሁሉ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዲና

ይህ የልያ ሴት ልጅ ስም ነው በዘፍጥረት 30:21 ይህን ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::(ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የወንዶችና የሴቶች ልጆች ቁጥር ሠላሣ ሶስት ነበር

እዚህ ወንዶች ልጆችና ሴቶች ልጆች የያዕቆብ ወንዶችና ሴቶች ልጆች እና የልያ የልጅ ልጆች ያመለክታል አት በአንድነት 33 ወንዶችና ሴቶች ልጆችና የልጅ ልጆች ነበረው (ቁጥሮች ይመልከቱ)

Genesis 46:16

ጽፎን… ሐጊ ሹኒ… ኤስቦን ዔሪ አሮዲና… አርኤሊ…ዩምና …የሱዋ የሱዊና… በሪዓ …ሐቤር… መልኪኤል

እነዚህ ሁሉ የወንድ ሰው ስሞች ናቸው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ሤራሕ

ይህ የሴት ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ዘለፋ

የልያ ሴት አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29:24 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ለያዕቆብ የወለደቻቸው እነዚህ ወንዶች ልጆች በአንድነት አሥራ ስድስት ናቸው

ይህ ከዘለፋ የተወለዱ አሥራ ስድስት ልጆች የልጅ ልጆችና የልጁ ልጅ ልጆች ናቸው (ቁጥሮች ይመልከቱ)

Genesis 46:19

አስናት

የሴት ስም ነው:: በዘፍጥረት 41:45 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ጶጥፌራ

የወንድ ስው ስም ነው:: በዘፍጥረት 41:45 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የኦን ካህን

ኦን የጸሐይ አምላክ ረሐ አምልዕኮ ማዕከል ያለባትና የጸሐይ ከተማ ደግሞም ሄልዮቱ የተባለች ከተማ ነች:: በዘፍጥረት 41:45 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቤላ ቤኬር አስቤል ጌራ ናዕማን አኪ ሮስ ማንፌን ሑፊምና አርድ

እነዚህ የወንድ ሰዎች ስሞች ናቸው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በአጠቀለይ አሥራ አራት ናቸው

ራሔል የወለደቻቸው 14 ወንዶችና የልጅ ልጆች ናቸው

Genesis 46:23

ሑሺም ያሕጽኤል ጉኒ ዬጽርና ሺሌም

እነዚህ የወንድ ሰዎች ስሞች ናቸው:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ባላ

የራሔል ሴት ባሪያ ወይም አገልጋይ ስም ነው:: በዘፍጥረት 29:29 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በአጠቃላይ ሰባት ነበሩ

ይህ ባላ የወለደቻቸው 7 ልጆችና የልጅ ልጆች እንደሆኑ ያመለክታል (ቁጥሮች ይመልከቱ)

Genesis 46:26

ስድሳ ስድስት

66 (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ሰባ

7ዐ (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

Genesis 46:28

በፊቱ የጌሤምን መንገድ እንዲያሳየው

የጌሜምን መንገድ እንዲያሳያቸው

ዮሴፍ ሰረገላውን አዘጋጀና … ወጣ

እዚህ “ዮሴፍ” አገልጋዮቹን ወይም ባሪያዎቹን ይወክላል:: አት “የዮሴፍ አገልጋዮች ሠረገላውን አዘጋጁለትና ዮሴፍም ….ወጣ” (ምትክ ቃላት ይጠቀሙ)

እስራኤልን ሊገናኘው …..ወጣ

“ወደ ላይ ወጣ” የሚለው ሀረግ የተጠቀመው ዮሴፍ አባቱን ሊገናኘው ወደ ከፍታማ ሥፍራ ስለተጓዘ ነው:: አት “እስራኤልን ሊገናኘው ሄዴ”

አንገቱን አቀፈና ረጅም ጊዜ አለቀሰ

እንገቱ ላይ ተጠመጠመና ረጅም ጊዜ አለቀሰ

አሁን ቢሞት እይቆጨኝ

“አሁን ለሞት ተዘጋጅቻለሁ” ወይም “አሁን እንግዲ የሚሞተው በደስታ ነው”

አንተ ገና በሕይወት ሳለህ ፊትህን አይቻለሁና

እዚህ “ፊት” ሙሉ ሰው ይወክላል”” ያዕቆብ ዮሴፍን በማየቱ የተሰማውን ደስታ ይገልጻል:: አት “አንተን እንደገና በሕይወት ስላየሁህ” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 46:31

የአባቱን ቤት

እዚህ ቤት ቤተሰቡን ይወክላል:: አት “የአባቱን ቤተሰብ” ወይም “የአባቱን ቤተሰዎች” (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

ወደ ፈርዖን ወጥቼ እናገረዋለሁ

ወደ አንድ ትልቅ ባለሥልጣን ሄዶ መናገር ወደ ላይ ወጣ የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነበር አት ለፈርዖን ለመናገር እሄዳለሁ

ለፈርዖን እነግረዋለሁ: ወንድምቼ … ያላቸውን ሁሉ

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስን ይዞአል ይህ በተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ወንድሞቼ …ያላቸውን ሁሉ… ለፈርዖን እነግረዋለሁ” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

Genesis 46:33

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ የተጠቀመው በታሪኩ ስለተከሰተው ዋና ክስተት ለማመልከት ነው፡፡ በቋንቋዎ ይህንን የሚገልጹበት መንገድ ካለ የጠቀሙ

ሥራችሁ ምንደነው ብሎ ቢጠይቃችሁ

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስን ይዞአል:: ይህ በተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ምን ሥራ ታከናውናላችሁ ብሎ ቢጠይቃችሁ” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

እንዲህ በሉት እኛ ባሪያዎችህ…. እኛም አባቶቻችንም…

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስን ይዞአል:: ይህ በተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “እንዲህ በሉት….እኛና አባቶቻችን ሁላችን…” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

የአንተ ባሪያዎች

የዮሴፍ ቤተሰቦች ለፈርዖን ሲናገሩ ራሳቸውን ባሪያዎችህ ብለው ማቅረብ አለባቸው:: ይህ ለአንድ ታላቅ ባለሥልጣን የሚነገርለት መንገድ ነው:: ይህም እንደ አንደኛ ወገን ሰው ሊገለጽ ይችላል:: አት “እኛ አገልጋዮችህ” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

በግ ጠባቂ ሁሉ ለግብጻዊያን ርኩስ/ ጸያፍ ነውና

“ጸያፍ” የሚለው ረቂቅ ስም “የሚያስጠላ” በሚለው ቅጽል ስም ሊተረጐም ይችላል:: አት “ግብጻዊያን የከብት ጠባቂዎችን እንደ ጸያፍ ይቆጥሩ ነበር” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)


Chapter 47

1 ዮሴፍም ወደ ፈርዖን ሄዶ፣ “አባቴና ወንድሞቼ በጎቻቸውን፣ ፍየሎቻቸውን እንዲሁም ያላቸውን ሁሉ ይዘው ከከነዓን አገር መጥተው በጌሤም ሰፍረዋል” አለው። 2 ከወንድሞቹም መካከል አምስቱን መርጦ፣ ፈርዖን ፊት አቀረባቸው። 3 ፈርዖን የዮሴፍን ወንድሞች፣ “ሥራችሁን ምንድነው?” ሲል ጠየቃቸው። እነርሱም ፈርዖንን፣ “እኛ አገልጋዮችህ ልክ እንደአባቶቻችን ከብት አርቢዎች ነን” አሉት። 4 ደግሞም፣ “በከነዓን ምድር ራቡ እጅግ የጸና በመሆኑ በጎችና ፍየሎች የሚሰማሩበት በማጣታቸው፣ ለጊዜው እዚህ ለመኖር መጥተናል፤ አሁንም ባሮችህ በጌሤም ምድር እንድንኖር እንድትፈቅድልን እንለምንሃለን” አሉት። 5 ፈርዖንም ዮሴፍን እንዲህ አለው፤ “አባትንህና ወንድሞችህ ወደ አንተ መጥተዋል፤ 6 የግብፅ ምድር እንደሆነ በእጅህ ነው፤ አባትህንና ወንድሞችህን ምርጥ በሆነው ምድር አስፍራቸው፤ በጌሤም ይኑሩ። ከመካከላቸው ልዩ ችሎታ ያላቸው መኖራቸውን የምታውቅ ከሆነ፣ የከብቶቼ ኅላፊዎች አድርጋቸው።” 7 ከዚህ በኋላ ዮሴፍ አባቱን ያዕቆብን ቤተ መንግሥት አግብቶ በፈርዖን ፊት አቀረበው፤ ያዕቆብ ፈርዖንን ከመረቀው በኋላ 8 ፈርዖን፣ “ለመሆኑ ዕድሜህ ምን ያህል ነው?” ሲል ያዕቆብን ጠየቀው። 9 ያዕቆብም ለፈርዖን፣ “በምድር ላይ በእንግድነት ያሳለፍሁት ዘመን 130 ዓመት ነው፤ ይህም አባቶቼ በእንግድነት ከኖሩበት ዘመን ጋር ሲነጻጸር አጭር ነው፤ ችግር የበዛበትም ነበር” ሲል መለሰለት። 10 ከዚያም ያዕቆብ ፈርዖንን መርቆ፣ ተሰናብቶት ወጣ። 11 ዮሴፍም አባቱንና ወንድሞቹን በግብፅ እንዲኖሩ አደረገ፤ ፈርዖን በሰጠውም ትእዛዝ መሠረት ምርጥ ከሆነው ምድር ራምሴን በርስትነት ሰጣቸው። 12 ዮሴፍም ለአባቱ፣ ለወንድሞቹና ለመላው የአባቱ ቤተ ሰዎች በልጆቻቸው ቁጥር ልክ ቀለብ እንዲሰፈርላቸው አደረገ። 13 በመላው ምድር እህል ባለመኖሩ ራቡ እየጸና ሄደ፤ ከዚህ የተነሣም ግብፅና ከነዓን በራብ እጅግ ተጎዱ፤ 14 ዮሴፍ የግብፅና የከነዓን ሰዎች እህል በመሸመት የከፈሉትን ገንዘብ ሁሉ ሰብስቦ ወደ ፈርዖን ቤተ መንግሥት አስገባ። 15 የግብፅና የከነዓን ሕዝቦችም ገንዘባቸው ባለቀ ጊዜ፣ ግብፃውያን ሁሉ ወደ ዮሴፍ ቀርበው፣ “የምንበላው እህል ስጠን፣ ገንዘባችን አልቆብናል፤ ዓይንህ እያየ እንዴት በራብ እንለቅ?” አሉት። 16 ዮሴፍም ከብቶቻችሁን አምጡ፣ ገንዘባችሁ ካለቀ በከብቶቻችህ ለውጥ እህል እሰጣችኋለሁ አለ። 17 ስለዚህ ከብቶቻቸውን ወደ ዮሴፍ አምጡ፤ እርሱም በፈረሶቻቸው፣ በበጎቻቸው፣ በፍየሎቻቸው፣ በከብቶቻቸውና በአህዮቻቸው ለውጥ እህል ሰጣቸው። በከብቶቻቸው ልዋጭ ባገኙት ምግብ በዚያ ዓመት ሳይራቡ እንዲያልፉ አደረጋቸው። 18 ያም ዓመት ካለፈ በኋላ ሕዝቡ በሚቀጥለው ዓመት ወደ ዮሴፍ መጥተው እንዲህ አሉት፣ “እንግዲህ ከጌታችን የምንሰውረው ምንም ነገር የለም፤ ገንዘባችን አልቆአል፤ ከብቶቻችንንም አስረክበንሃል፤ እንግዲህ ለጌታችን የምንሰጠው፣ ከሰውነታችንና ከመሬታችን በቀር ሌላ ምንም ነገር የለንም። 19 ታዲያ እያየኸን እንዴት እንለቅ? መሬታችንም ለምን ጠፍ ሆኖ ይቅር? እኛንና መሬታችንን ውሰድና በለውጡ እህል ስጠን፤ እኛ የፈርዓን አገልጋዮች እንሆናለን፤ መሬታችንም የእርሱ ይሁን፣ እኛም እንዳንሞት መሬታችንም ጠፍ ሆኖ እንዳይቀር የምንዘራው ዘር ስጠን። 20 ስለዚህ ዮሴፍ የግብፅን ምድር ሁሉ ለፈርዖን ገዛለት፤ ራቡም እጅግ ስለጸናባቸው ግብፃውያን ሁሉ መሬታቸውን ሸጡ፣ ምድሪቱም የፈርዖን ርስት ሆነች። 21 ዮሴፍ በግብፅ አገር ዳር እስከ ዳር ያሉት ሰዎች ሁሉ የንጉሡ አገልጋዮች እንዲሆኑ አደረገ። 22 ሆኖም ዮሴፍ የካህናቱን መሬት አልገዛም፤ ምክንያቱም ካህናቱ ከፈርዖን ቋሚ አበል ስለሚያገኙ እርሱም ከሚሰጣቸው አበል ምግብ ያገኙ ስለነበረ መሬታቸውን አልሸጡም። 23 ዮሴፍ ሕዝቡን እንዲህ አላቸው፣ “እነሆ፣ ዛሬ እናንተንም መሬታችሁንም ለፈርዖን ገዝቻችኋለሁና ይህን ዘር ወስዳችሁ በመሬት ላይ ዝሩ። 24 መከሩ በሚሰበሰብበት ጊዜ ግን ከአምስት እጅ አንዱን ለፈርዖን ታስገባላችሁ፣ ከአምስት እጅ አራቱን ደግሞ ለመሬታችሁ ዘር፣ እንዲሁም ለራሳችሁ፣ ለቤተ ሰቦቻችሁና ለልጆቻችሁ ምግብ ታደርጉታላችሁ።” 25 እነርሱም፣ “እንግዲህ ሕይወታችንን አትርፈህልናል፤ በጌታችን ፊት ሞገስ ካገኘን ለፈርዖን ገባሮች እንሆናለን” አሉት። 26 ስለዚህ ዮሴፍ የምርቱ አንድ አምስተኛ ለፈርዖን እንዲገባ የሚያዝ የመሬት ሕግ አወጣ፤ ይህም ሕግ እስከ ዛሬ ይሠራበታል። በፈርዖን እጅ ያልገባው መሬት የካህናቱ ብቻ ነው። 27 በዚህ ጊዜ እስራኤላውያን በግብፅ አገር በጌሤም ይኖሩ ነበር፣ በዚያም ሀብት ንብረት አፈሩ፤ ቁጥራቸውም እጅግ እየበዛ ይሄድ ጀመር። 28 ያዕቆብ በግብፅ ዐሥራ ሰባት ዓመት ኖረ፣ ዕድሜውም አንድ መቶ አርባ ሰባት ዓመት ነበር። 29 እስራኤልም የሚሞትበት ጊዜ መቃረቡን እንደተረዳ ልጁን ዮሴፍን አስጠርቶ እንዲህ አለው፤ “በአንተ ዘንድ ሞገስ ካገኘሁ እጅህን በጭኔ ላይ አኑረህ፣ በጎነትንና ታማኝነትን ልታደርግልኝ ቃል ግባልኝ፤ በምሞትበት ጊዜ በግብፅ አትቅበረኝ፤ 30 እኔም ከአባቶቼ ጋር ሳንቀላፋ ከግብፅ አውጥተህ እነርሱ በተቀበሩበት ቦት ቅበረኝ” ዮሴፍም፣ “እሺ፣ እንዳልኸኝ አደርጋለሁ” አለ። 31 ያዕቆብ፤ “በል ማልልኝ” አለው። ዮሴፍም ማለለት፣ እስራኤልም በአልጋው ራስጌ ላይ ሆኖ ጎንበስ አለ።



Genesis 47:1

ዮሴፍ ሄዶ ለፈርዖን ነገረው ….ከወንድምቹም አምስት ሰዎችን ወስዶ በፈርዖን ፊት አቀረባቸው

UDB ክስተቶች በቅደም ተከተል ሲያስቀምጥ ULB ጸሐፊው እንዳስቀመጠ ይዘረዝራል (የክስተቶች ቅደም ተከተል ይመልከቱ)

Genesis 47:3

እኛ ባሪያዎችህ የበግ አርቢዎች ነን

ባሪያዎችህ በጎችን እናረባለን

ባሪያዎችህ

የዮሴፍ ወንድምች ራሳቸውን እንደ “ባሪያዎችህ” ያቀርቡታል:: ይህ ብዙ ኃላፊነት ላለው ሰው የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው:: ይህም እንደ አንደኛ ወገን ሰው ሊገለጽ ይችላል:: አት “እኛ ባሪያዎችህ ወይም እኛ” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

እንደ አባቶቻችን

“እኛና ቅድመ አባቶቻችን ሁላችን” ወይም “እኛና አባቶቻችን ሁሉ”

በዚህ ምድር ለጊዜው ለመኖር መጥተናል

በግብጽ ለጊዜው ለመኖር መጥተናል

በጎች የሚሠማሩበት ሥፍራ የለምና

በጎች የሚሠሩበት ሣር የለምና

አሁንም

ይህ በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም ነገር ግን ለሚቀጥለው ዋና ነገር ትኩረት ለመስጠት ነው::

Genesis 47:5

የግብጽ ምድር በፊትህ ናት

“የግብጽ ምድር ለአንተ ክፍት ነው” ወይም “መላው የግብጽ ምድር በአንተ እጅ ነው”

በመልካም ምድር አባትህንና ወንድሞችህን አኑራቸው በጌሤም ምድር

አባትህንና ወንድሞችህን ምርጥ በሆነው በጌሤም ምድር አኑራቸው

ከመካከላቸው ልዩ ችሎታ ያላቸው መኖራቸውን የምታውቅ ከሆነ

ይህ የሚገለጸው ከብት የማርባት ችሎታ እንዳላቸው ነው:: አት “ከመካከላቸው ከብት በማርባት ትልቅ ችሎታ ያላቸውን የሚቃውቅ ከሆነ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 47:7

ያዕቆብ ፈርዖንን ባረከው

እዚህ “ባረከው” የሚለው ለዚያ ሰው አዎንታዊና ጠቃሚ ነገሮች እንዲሆኑለት መሻቱን ገለጸ ማለት ነው

እድሜህ ምን ያህል ነው?

እድሜህ ስንት ዓመት ነው?

የእንግድነቴ ዘመን መቶ ሠላሣ ዓመት ነው

የእንግድነቴ ዘመን የሚለው ሀረግ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በመዘዋወር በምድር ላይ ምን ያህል እንደኖረ ያመለክታል:: አት “በምድር ላይ በእንግድነት ያሳለፍኩት ዘመን 13ዐ ዓመት ነው” (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

የሕይወቴ ዘመኖች አባቶቼ በእንግድነት ከኖሩበት ዘመን ጋር ሲነጻጸር ጥቂት ናቸው

ከአብርሃምና ከይስሐቅ የሕይወት ዘመን ጋር ስነጻጸር ዮሴፍ የሕይወቱ ዘመን አጭር እንደሆነ ይናገራል

ችግር የበዛበት

ያዕቆብ በሕይወቱ ብዙ ሥቃይና ችግር ተለማምዶአል

Genesis 47:11

ዮሴፍም አባቱንና ወንደሞቹን አኖረ

ከዚያም ዮሴፍ አባቱንና ወንድሙን ተንከባከባቸው በሚኖሩበት ሥፍራ እንዲመሠረቱ አደረገ

ራሚሴ ምድር

ይህ የጐሼም ምድር ሌላው ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በየልጆቻቸው ቁጥር

እዚህ “ልጆች” በቤተሰብ ጥገኝነት ያሉ ትናንሽ ልጆች ማለት ነው:: አት “በየቤተሰቡ በሚገኙ ትናንሽ ልጆች ቁጥር”

Genesis 47:13

አሁንም

ይህ ቃል ዋናው ታሪክ በመሃል የሚቋረጥበትን ለማመልከት ተጠቅሞአል:: በዚህ ጸሐፊው የታሪኩን አድስ ክፍለ መናገር ይጀምራል::

የግብጽ ምድርና የከነዓን ምድር

ይህ በእነዚህ አገሮች የሚኖሩ ሰዎችን ያመለክታል አት የግብጽ ሰዎችና የከነዓን ሰዎች (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

ተጐዳ

ተቀጨ ወይም ደከመ

ዮሴፍም በግብጽ ምድርና በከነዓን ምድር በእህል ሸመት የተገኘውን ገንዘብ ሰበሰበ

ዮሴፍም የግብጽና የከነዓን ሰዎች ገንዘባቸውን ሁሉ ከዮሴፍ እህል ለመሸመት አውለዋል

ዮሴፍም ሰበሰበ… ዮሴፍም አመጣ

ገንዘቡን እንዲሰበስቡና እንዲያመጡ ዮሴፍ አገልጋዮቹን እንዳዘዘ ይገመታል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

Genesis 47:15

የግብጽና የከነዓን ምድር ገንዘብ ባለቀ ጊዜ

እዚህ ምድር በዚያ ምድር የሚኖሩ ሰዎችን ይወክላል:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት “የግብጽና የከነዓን ሕዝቦችም ገንዘባቸው ባለቀ ጊዜ” (ምትከ ቃላት አጠቃቀምና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የግብጽና የከነዓን ምድሮች

ከግብጽ ምድር እና ከከነዓን ምድር

ብሩ አልቆብናልና በፊትህ ስለምን እንሞታለን?

ሰዎች እህል ለመሸመት እንዴት እንደጓጉ ትኩረት ለመሰጠት ጥቃቄ ይጠቀማሉ፡፡ ይህ ጥያቄ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊተረጐም ይችላል፡ አት “ገንዘባችን ስላለቀብን እባካችሁ እንድንሞት አታድርጉ!” (ሽንገላ አዘል አግናኝ ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

እህልን መገባቸው

እህል ምግብን በአጠቃላይ ይወክላል:: አት “እህልን ሰጣቸው” ወይም “እህልን አደላቸው” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 47:18

እነርሱም ወደ እርሱ መጡ

ሰዎች ወደ ዮሴፍ መጡ

እኛ ከጌታችን አንሰውርም

ሰዎችን ዮሴፍን እንደ” ጌታችን” ያመለክታሉ ይህ ትልቅ ሥልጣን ላሌው ሰው የሚነገርለት መደበኛ መንገድ ነው:: ይህ እንደ ሁለተኛ ወገን ሰው ሊገለጽ ይችላል:: አት” ከጌታችን የምንሰውረው የለም” ወይም “ከአንተ የምንሰውረው የለም” (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

በጌታችን ፊት አንዳች የቀረ የለም

እዚህ ፊት ዮሴፍን ያመለክታል:: አት “ለጌታችን የምንሰጠው የቀረ የለንም” (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

እኛ በዐይኖችህ ፊት ስለምን እንሞታለን? ምድራችንስ ስለምን ትጠፋለች?

እዚህ ዐይኖች የዮሴፍን እይታ ያመለክታሉ ሰዎች እህልን ለመግዛት ምንኛ እንደጓጉ ለማተኮር ጥያቄ ይጠቀማሉ ይህ ጥያቄ እንደ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: አት “እኛ ስንሞት ምድራችም ስትጐዳ እባክህን እንዲሁ ዝም ብለህ አትመለከተን” (ምትክ ቃላት አጠቃቀምና ሽንገላ አዘል አግናኝ ጥያቄዎችን ይጠቀሙ)

እኛ ለምን እንሞታለን እኛና ምድራችን

የተዘራበት ዘር ስለሌለባት ምድሪቱ የተጐዳችና ጥቅም የሌላት መሆንዋ ምድሪቱ እንደሚትሞት ተደርጐ ተነግሮአል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 47:20

በዚህ መንገድ የግብጽ ምድር ሁሉ ለፈርዖን ገዛለት

ስለዚህ ምድሪቱ የፈርዖን ሆነች

ዮሴፍ ያልገዛው የካህናቱን መሬት ብቻ ነበር

ነገር ግን የካህናቱን መሬት አልገዛም

ካህናቱ ድርጐ ያግኙ ነበር

ድርጐ በቋሚነት አንድ ሰው ለሌላ ሰው የሚሰጠው የገንዘብ ወይም የመግብ መጠን ነው:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ፈርዖን በየዕለቱ ለካህናት የተወሰነ ምግብ ይሰጥ ነበር” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እነርሱም ፈርዖን ከመደበላቸው ይመገቡ ነበር

ፈርዖን ከሰጣቸው ይመገቡ ነበር

Genesis 47:23

በመሬት ላይ ዝሩ

ሊትዘሩ ትችላላችሁ

በመከርም ጊዜ ፍሬውን ከአምስቱ እጅ አንዱን እጅ ለፈርዖን ስጡ አራቱም እጅ ለእናንተ ለራሳችሁ ይሆናል

አምስት እጅ የሚለው ቃል ክፍልፋይ ነው፡፡ አት “በመከር ጊዜ እህላችሁን በአምስት መደብ ትከፍላላችሁ አንዱን መደብ እንደክፍያ ለፈርዖን ትሰጡታላችሁ እናም አራቱ መደቦች ለእናንተ ይሆናሉ” (ክፍልፋዮችን ይመልከቱ) ለቤተሰቦቻችሁና ለልጆቻችሁ ምግብ ታደርጉታላችሁ (የተደበቁትን ስለመግልጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 47:25

በዐይኖችህ ፊት ሞገስ ካገኘን

ሞገስ ማግኘት የሚለው ሀረግ በአንድ ሰው ተቀባይነትን ማግኘት የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው:: ደግሞም ዐይኖች ማየትንና ማየት ሃሳብንና በየናን ይወክላል:: አት “በእኛ ከተደሰትክ” (ፈሊጣዊና ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በግብጽ ምድር

“በግብጸ ምድር ላይ” ወይም “በመላው የግብጽ ምድር”

እስክ ዛሬ ድረስ

ጸሐፊው እስከጻፈበት ጊዜ ድረስ

አንድ አምስተኛ

በዘፍጥረት 47:24 አንድ እምስተኛ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

Genesis 47:27

ንብረትንም አፈሩ እጅግም በዙ

በዙ የሚለው ቃል እንዴት እንደአፈሩ ይገልጻል እነርሱም ብዙ ልጆች ነበሩአቸው (ድርብ ቃላት ይመልከቱ)

ፍሬያማ ነበሩ

እዚህ ፍሬያማ መበልጸግ ወይም ብዙ ልጆች መኖር ማለት ነው

አሥራ ሰባት ዓመታት

17 ዓመታት (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

የያዕቆብም የሕይወቱ ዘመን አንድ መቶ አርባ ሰባት ዓመት ነበር

ያዕቆብ የኖረው 147 ዓመት ነው (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

Genesis 47:29

እስራኤልም የሚሞትበት ጊዜ መቃረቡን

ይህ ጊዜ እንደሚጓዝና አንድ ቦታ እንደሚመጣ ይናገራል:: አት “እስራኤል የሚሞትበት ጊዜ እንደደረሰ” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

በዓይኖችህ ፊተ ሞገስን ካገኘሁ

እዚህ ዓይኖች የማየት ምትክ ቃል ነው እናም ማየት ሃሳብን ወይም አመለካከትን ይወክላል:: አት “በአንተ ፊት ሞገስ ካገኘሁ ወይም ካስደሰትኩህ” (ምትክ ቃላትና ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አሁን

ይህ በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም ለሚቀጥለው ጠቃሚ ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ነው

ሞገስ ማግኘት

አንድ ሰው በአንድ ሰው ተቀባይነቱን ማረጋገጥ ማለት ነው ፈሊጣሊ አነጋገር ይመልከቱ

እጅህን ከጭኔ በታች አድርግ

ለጠንቃቃ ቃል መግባት የሚደረግ ምልክት ነው በዘፍጥረት 24:2 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

በጐነትንና ታማኝነትን ሊታደርግልኝ

በጐነት እና ታማኝነት የተባሉ ረቂቅ ስሞች እንደ ቅጽል ስሞች ሊተረጐሙ ይችላሉ አት በበጐነትና በታማኝነት አድርግልኝ ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ

እባክህን በግብጽ አትቅበረኝ

እባክህን የሚለው ለዚህ ጥያቄ እጽንዖት ይሰጣል

ከአባቶቼ ጋር ሳንቀላፋ

ማንቀላፋት መሞትን ለዘብ ባለ ቃል የሚገልጽ ነውፀፀ አት “በሚሞትበትና ከዚህ ቀደም የሞቱ ቤተሰቦቼን በሚገናኝበት ጊዜ” (ንኀብነት ወይም ለዘብ ባለና በተዘዋዋሪ መንገድ አንድን ነገር የመግልጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ቃል ግባልኝ

“ተስፋ ስጠኝ” ወይም “ማልልኝ”

ማለለት

“ተስፋ ሰጠው” ወይም “ቃል ገባለት”


Chapter 48

1 ከጥቂት ጊዜ በኋላም፣ “አባትህ ታሞአል” ተብሎ ለዮሴፍ ስለተነገረው ሁለቱን ልጆቹን ምናሴንና ኤፍሬምን ይዞ ሄደ። 2 ለያዕቆብ፣ “ልጅህ ዮሴፍ ወደ አንተ መጥቶአል” ተብሎ በተነገረው ጊዜ፣ እስራኤል ተበረታትቶ አልጋው ላይ ተቀመጠ። 3 ያዕቆብም ዮሴፍን እንዲህ አለው፤ “ሁሉን የሚችል አምላክ በከነዓን ምድር ሎዛ በምትባል ቦታ ተገለጠልኝ፤ ባረከኝም፤ 4 እንዲህም አለኝ፤ ‘ፍሬያማ አደርግሃለሁ፣ ዝርያዎችህም ብዙ ሕዝቦች ይሆናሉ፣ ይህችንም ምድር ለዝርያዎችህ ለዘላለም ርስት አድርጌ እሰጣቸዋለሁ’ አለኝ።” 5 ወደዚህ ከመምጣቴ በፊት በግብፅ የወለድሃቸው ሁለቱ ልጆችህ ከእንግዲህ የእኔ ልጆች ሆነው ይቆጠራሉ፤ ሮቤልና ስምዖን ልጆቼ እንደሆኑ ሁሉ፣ ኤፍሬምና ምናሴም ልጆቼ ይሆናሉ። 6 ከእነርሱ በኋላ የሚወለዱልህ ልጆች ግን፣ የአንተ ይሁኑ፤ በርስት ድልድላችው ግን በወንድሞቻቸው ስም ይቆጠራሉ። 7 ከሰሜን ምዕራብ መስጴጦምያ ስመለስ ኤፍራታ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረኝ፤ እናትህ ራሔል በከነዓን ምድር ሞታብኝ አዘንሁ። እኔም ወደ ኤፍራታ ማለት ወደ ቤተ ልሔም በሚወስደው መንገድ ዳር ቀበርኋት።” 8 እስራኤልም የዮሴፍን ልጆች ባየ ጊዜ፣ “እነዚህ እነማን ናቸው?” ሲል ጠየቀ፤ 9 ዮሴፍም፣ “እነዚህ እግዚአብሔር የሰጠኝ ልጆች ናቸው” ብሎ መለሰለት፤ እስራኤልም “አቅርባቸውና ልመርቃቸው” አለ። 10 በዚህ ጊዜ እስራኤል ዓይኖቹ በእርጅና ምክንያት በመድከማቸው አጥርቶ ማየት ይሳነው ነበር፤ ስለዚህ ዮሴፍ ልጆቹን አባቱ ዘንድ አቀረባቸው፤ አባቱም ስሞ አቀፋቸው። 11 እስራኤልም ዮሴፍን፣ “ዓይንህን እንደገና ዐያለሁ ብዬ አላሰብኩም ነበር፤ እግዚአብሔር ግን ልጆችህን ጭምር ለማየት አበቃኝ” አለው። 12 ዮሴፍም ልጆቹን ከእስራኤል ጉልበት ፈቀቅ በማድረግ አጎንብሶ በግንባሩ መሬት ላይ ተደፋ። 13 ከዚያም ዮሴፍ ሁለቱን ልጆቹን ይዞ ኤፍሬምን ከራሱ በስተቀኝ ከእስራኤል በስተግራ፣ ምናሴን ደግሞ ከራሱ በስተግራ ከእስራኤል በስተቀኝ በኩል አቀረባቸው። 14 እስራኤል ግን ቀኝ እጁን በታናሹ በኤፍሬም ራስ ላይ አኖረ፣ ግራ እጁንም በቀኝ እጁ ላይ አስተላልፎ በበኩሩ በምናሴ ላይ አኖረ። 15 ከዚህ በኋላ ዮሴፍን ባረከ፤ እንዲህም አለው፤ “አባቶቼ አብርሃምና ይስሐቅ መንገዱን በመከተል ያገለገሉትና ለእኔም እስከ ዛሬ ድረስ በዘመኔ ሁሉ እረኛ የሆነኝ አምላክ፣ 16 ከጉዳትም ሁሉ የታደገኝ ምልአክ፣ እርሱ እነዚህን ልጆች ይባርክ፤ እነርሱም በስሜ፣ በአባቶቼ በአብርሃምና በይስሐቅ ስም ይጠሩ፣ በምድር ላይ እጅግ ይብዙ። 17 ዮሴፍ አባቱ ቀኝ እጁን በኤፍሬም ራስ ላይ ማድረጉን ሲያይ ቅር ተሰኘ፤ ከኤፍሬም ራስ ላይ አንስቶ በምናሴ ራስ ላይ ለማኖር የአባቱን እጅ ያዘ፤ 18 ዮሴፍም፣ “አባቴ ሆይ፣ እንዲህ አይደለም በኩሩ ይህኛው ስለሆነ፣ ቀኝ እጅህን እርሱ ራስ ላይ አድርግ” አለው። 19 አባቱ ግን፣ “ዐውቃለሁ፣ ልጄ ዐውቃለሁ፣ እርሱም እኮ ሕዝብ ይሆናል፤ ታላቅም ይሆናል፤ ይሁን እንጂ፣ ታናሽ ወንድሙ ከእርሱ ይበልጣል፤ ዘሮቹም ታላቅ ሕዝቦች ይሆናሉ” ብሎ እምቢ አለው። 20 በዚያን ዕለት ባረካቸው፣ እንዲህም አላቸው፤ “እስራኤላውያን በሚመርቁበት ጊዜ የእናንተን ስም በማስታወስ፤ ‘እግዚአብሔር እንደ ኤፍሬምና እንደ ምናሴ ያድርጋችሁ’ ይላሉ” በዚህ ሁኔታም ኤፍሬምን ከምናሴ አስቀደመው። 21 ከዚህ በኋላ እስራኤል ዮሴፍን እንዲህ አለው፣ እኔ የምሞትበት ጊዜ ተቃርቦአል፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሆናል፤ ወደ አባቶቻችሁም ምድር መልሶ ያገባችኋል። 22 እነሆ በሰይፌና በቀስቴ ከአሞራውያን እጅ የወሰድኋትን ምድር ከወንድሞችህ ድርሻ አብልጬ ለአንተ ሰጥቼሃለሁ።”



Genesis 48:1

እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ የታሪኩ አድስ ክፍል መጀመሩን ለማመልከቱ ተጠቅሞአል (አድስ ክስተት ስለማስታወቅ ይመልከቱ)

አንድ ሰው ለዮሴፍ ተናገረው

አደ ሰው ለዮሴፍ ነገረው

እየው፤ አባትህ

ስማ ፤አባትህ፤ እዚህ “እየው” የሚለው ቃል የዮሴፍን ትኩረት ለማግኘት ተጠቅሞአል::

ስለዚህ ይዞ

ስለዚህ ዮሴፍ ይዞ

ለያዕቆብ … በተነገረው ጊዜ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት “አንድ ሰው ለያዕቆብ በነገረው ጊዜ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ልጅህ ዮሴፍ ልያይህ ወደ አንተ መጥቶአል

ልጅህ ዮሴፍ መጥቶአል

እስራኤል ተበረታትቶ በአልጋው ላይ ተቀመጠ

እዚህ እስራኤል ተነሥቶ በአልጋው ሊቀመጥ የታገለውን አንድ ሰው አንድን ዕቃ እንደሚሰበስብ ብርታትን እንደሰበሰበ አድርጐ ጸሐፊው ይናገራል:: አት “በአልጋው ተነሥቶ ሊቀመጥ እስራኤል ከፍተኛ ጥረት አድርጐአል ወይም በአልጋው ተነሥቶ ሊቀመጥ እስራኤል ታግሎአል” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይጠቀሙ)

Genesis 48:3

ሎዛ

ይህ የከተማ ስም ነው:: በዘፍጥረት 28:19 የዚህን ከተማ ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በከነዓን ምድር … ባረከኝም እንዲህም አለኝ

ይህ በሌላ ሀረግ እንደሚጀምር እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: “በከነዓን ምድር ባረከኝ እናም እንዲህ አለኝ”

ባረከኝ

እግዚአብሔር መደበኛ በረከትን በአንድ ሰው ላይ እንዳደረገ ያመለክታል

እንዲህም አለኝ እነሆ ፍሬያማ አደርግሃለሁ አበዛሃለሁ ለብዙ ሕዝብም ጉባዔ አደርግሃለሁ ይህችንም ምድር ከአንተ በኋላ ለዘላለም ርስት ለዘርህ እሰጣታለሁ

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስን ይዞአል እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል አት ፍሬያማ እንደሚያደርገኝና እንደሚያበዛች ተናግሮኛል:: እናም ለብዙ ሕዝብም ጉባዔ እንደሚያደርገኝና ይህችንም ምድር ከእኔ በኋላ ለዘላለም ርስት አድርጐ ለዘሬ እንደሚሰጠኝ ነግሮኛል (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

እነሆ

እዚህ ቦታ እነሆ የተጠቀመው እግዚአብሔር ሊናገር ስላለው ነገር ያዕቆብ ትኩረት እንዲሰጥ ለማንቃት ነው

ፍሬያማ አደርግሃለሁ አበዛሃለሁ

አበዛሃለሁ የሚለው ሀረግ እግዚአብሔር እንዴት ያዕቆብን ፍሬያማ እንደሚያደርገው ይገልጻል:: አት “ብዙ ዘር/ትውልድ እሰጥሃለሁ” (ድርብ ቃላትና ፈሊጣዊ አነጋገር ይጠቀሙ)

አንተን ለብዙ ሕዝብ ጉባዔ አደርግሃለሁ

እዚህ አንተ ያዕቆብን ቢያመለክትም የያዕቆብን ትውልድ ይወክላል አት “ትውልድህን ብዙ ሕዝቦች አደርጋለሁ” (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

የዘላለም ርስት

ቋሚ ርስት

Genesis 48:5

አሁን

ይህ በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም ነገር ግን ለሚቀጥለው ዋና ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ተጠቅሞአል

ኤፍሬምና ሚናሴ ለእኔ ናቸው

እንደ ዮሴፍ ወንድሞች ኤፍሬምና ሚናሴ ከምድሪቱ ክፍል የየራሳቸውን ርስት ይቀበላሉ

በርስታቸው በወንድሞቻቸው ስም ይጠራሉ

ተገቢ ትርጉሞች የሚከተሉት ናቸው 1 እንደ ሚናሴና ኤፍሬም ነገዶች ሌሎች የዮሴፍ ልጆች ምድሪቱን ይወርሳሉ 2 ዮሴፍ ከኤፍሬምና ሚናሴ የተለየ ምድር የሰጠዋል እናም የዮሴፍ ሌሎች ልጆች ያን ምድር ይወርሳሉ አት በርስት ድልደላቸው በወንድሞቻቸው ስም ይቆጠራሉ

ኤፍራታ

ይህ የቤተልሔም ከተማ ስም ነው:: በዘፍጥረት 35:16 የዚህን ከተማ ስም እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ያም ቤተልሔም ነው

ጸሐፊው የዳራ መረጃ ይሰጣል (የዳራ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 48:8

እነዚህ እነማን ናቸው?

እነዚህ የማን ወንዶች ልጆች ናቸው?

ባረካቸው

አባት ልጆቹንና የልጅ ልጆቹን እብዛኛውን ጊዜ መደበኛ በረከት ይባርካል

በዚህን ጊዜ የእስራኤል ዐይኖች …. ማየት ተስኖአቸው

በዚህን ጊዜ የሚለው ቃል የተጠቀመው ታሪኩ ወደ እስራኤል ዳራ መረጃ እንደተቀየረ ለማመልከት ነው (ዳራ መረጃ ይመልከቱ)

እርሱም ሳማቸው

እስራኤል ሳማቸው

Genesis 48:11

ፊትህን እንደገና አያለሁ

እዚህ “ፊት” ሙሉ ሰው ይወክላል:: አት እንደገና አይሃለሁ (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን አንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በእስራኤል ጉልበቶች መካከል

ዮሴፍ ልጆቹን በእስራኤል ጭን ወይም ጉልበት ላይ ማስቀመጡ እስራኤል እንደራሱ ልጆች እንደተቀበላው የሚገልጽ ምልክት ነው:: ይህም ለልጆች የወራሽነት መብት ከያዕቆብ ያስገኛል (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

በግምባሩም ወደ ምድር አጐንብሶ ሰገደ

ዮሴፍ ለአባቱ ክብርን ለመስጠት ወደ ምድር አጐንበሶ ሰገደ (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

ሚናሴንም በግራው በእስራኤል ቀኝ

እስራኤል ቀኝ እጁን በሚናሴ ላይ እንዲያደርግ ዮሴፍ ልጆቹን ያስቀምጣቸዋል ሚናሴ ታላቅ ወንድም ነው እናም ቀኝ እጅ ትልቅ በረከት የመቀበል ምልክት ነው (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Genesis 48:14

ቀኝ እጁን ዘርግቶ በኤፍሬም ራስ ላይ አኖረ

ቀኝ እጁን በኤፍሬም ራስ ላይ ማኖር እርሱ ትልቅ በረከት እንዲቀበል ምልክት ነበር (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

እስራኤል ዮሴፍን ባረከው

ዮሴፍ ደግሞ ኤፍሬምንና ሚናሴን ይወክላል:: ዮሴፍ አባት ስለሆነ እርሱ ብቻውን ተጠቅሶአል (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

አባቶቼ አብርሃምና ይስሐቅ በፊቱ የሄዱለት እግዚአብሔር

እግዚአብሔርን ማገልገል በእግዚአብሔር ፊት እንደመሄድ ተደርጐ ተነግሮአል አት አያቴ አብርሃምና አባቴ ይስሐቅ ያገለገሉት እግዚአብሔር (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እረኛ የሆነኝ

እረኛ በጐቹን እንደምንከባከብ እግዚአብሔር እስራኤልን ተንከባክቦታል አት እረኛ እንስሳትን እንደሚንከባከብ የተንከባከበኝ (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

መልአክ

ተገቢ ትርጉሞች አት እግዚአብሔር ያዕቆብን ለመጠበቅ የላከውን መልአክ ያመለክታል 2 ይህ እግዚአብሔር ያዕቆብን ለመጠበቅ በመልአክ መልክ የተገለጸውን ያመለክታል

ጠበቀኝ

አዳነኝ

ስሜም የአባቶቼ የአብርሃምና የይስሐቅ ስም በእነርሱ ይጠራ

እዚህ ስም ሰውን ይወክላል ስሜ በእነርሱ ይጠራ የሚለው ሀረግ አንድ ሰው ከሌላ ሰው የተነሣ እንዲታወስ የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ከኤፍሬምና ሚናሴ የተነሣ ሰዎች አብርሃም ይስሐቅንና እኔን ያስታውሱ” (ምትክ ቃል : ፈሊጣዊ አነጋገርና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በምድርም ላይ ይብዙ

እዚህ እነርሱ ኤፍሬምንና ሚናሴን ቢያመለክትም የእነርሱ ትውልድንም ይወክላል:: አት “በምድር ሁሉ ላይ የሚኖር ብዙ ትውልድ ይኑራቸው” (ምትክ ቃል እጠቃቀም ይመልከቱ)

Genesis 48:17

ቀኝ እጅህን እርሱ ራስ ላይ አድርግ

ቀኝ እጅ በኩር ወንድ ልጅ የሚያገኘው ትልቅ በረከት ምልከት ነበር (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Genesis 48:19

እርሱ ደግሞ ሕዝብ ይሆናል ታላቅም ይሆናል

እዚህ እርሱ ሚናሴን ቢያመለክትም የእርሱን ትውልድ ይወክላል አት ታላቅ ልጅህ ብዙ ትውልድ ይኖረዋል እናም ታላቅ ሕዝብ ይሆናል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

በዚያን ቀን በእነዚህ ቃላት

በዚያ ዕለት እንዲህ ብሎ

በእናንተ ስም እስራኤል እንዲህ ብሎ ይባርካል

የእስራኤልም ሰዎች ሌሎችን በሚባርኩበት ጊዜ በስማችሁ ይባርካሉ

በእናንተ ስም እንዲህ ብለው እግዚአብሔር እንደ ኤፍሬምና እንደሚናሴ ያድርጋችሁ

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስን ይዞአል ይህም እንደ ተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “በእናንተ ስም እግዚአብሔር ሌሎችን ሰዎች እንደ ኤፍሬምና እንደ ሚናሴ እንዲያደርግ ይጠይቁታል” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥ ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

እንደ ኤፍሬምና እንደ ሚናሴ

እስራኤል ኤፍሬምን አስቀድሞ መጥራቱ ኤፍሬም ከሚናሴ ታላቅ እንደሚሆን የሚገልጽ ነው

እስራኤል ኤፍሬምን ከሚናሴ አስቀድሞታል

ለኤፍሬም ትልቁን በረከት መስጠትና ኤፍሬም ከሚናሴ የተሻለ አድርጐ መውሰድ እስራኤል በአካል ኤፍሬምን ከሚናሴ በፊት እንዳስቀመጠው ተደርጐ ተገልጾአል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 48:21

ከእናንተ ጋር ይሆናል ወደ አባቶቻችሁም ምድር መልሶ ያገባችኋል

እዚህ “እናንተ” “የእናንተ” ብዙና የእስራኤልን ሕዝብ ሁሉ ያመለክታል (“እናንተ” አጠቃቀም ይመልከቱ)

ከእናንተ ጋር ይሆናል

እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ እንደሚረዳና እንደሚባረካቸው የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው አት እግዚአብሔር ይረዳችኋል ወይም እግዚአብሔር ይባርካችኋል (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ወደ አባቶቻችሁም ምድር

ወደ ዘራችሁም ወይም ትውልዳችሁም ምድር

ለአንተ ከወንድሞችህ አንድ እጅ እብልጬ ዐምባ ሰጠሁህ

ተገቢ ትርጉሞች 1 ከወንድሞቹ ይበልጥ ብዙ ክብርና ሥልጣን ለዮሴፍ መሰጠቱ እርሱ በአካል ከሌሎች የበላይ ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “ለአንተ ከሌሎች ለሚትበልጠው የተራራውን ዐምባ ሰጠሁህ” ወይም 2)ያዕቆብ ለዮሴፍ ወንድሞች ከሚሰጠው መሬት በላይ ለዮሴፍ እንደሚሰጠው ይገልጻል:: አት “ለአንተ ለወንድሞችህ ከሰጠሁት በላይ ridge ሰጠሁህ የተራራውን ዐምባ ሰጠሁህ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ለአንተ

እዚህ አንተ በነጠላ የተገለጸና ዮሴፍን ያመለክታል (አንተ አጠቃቀም ይመልከቱ)

በሰይፌና በቀስቴ ከአሞራዊያን እጅ የወሰድኳትን ዐምባ

እዚህ ሰይፍ እና ቀስት በጦርነት መዋጋትን ያመለክታሉ፡፡ አት “የተዋጋሁትና ከአሞራዊያን እጅ የወሰድሁት ምድር” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)


Chapter 49

1 ያዕቆብ ልጆቹን ጠርቶ እንዲህ አላቸው፤ “በአንድነት ተሰብሰቡና ወደፊት የሚገጥማችሁን ነገር ልንገራችሁ፣ 2 እናንተ የያዕቆብ ልጆች፣ በአንድነት ተሰብስባችሁ ስሙ፣ አባታችሁ እስራኤል የሚነግራችሁንም አድምጡ። 3 ሮቤል፣ ኃይልና የጎልማሳነት ብርታት በነበረኝ ጊዜ የወለድሁህ የበኩር ልጄ ነህ። ከልጆቼ ሁሉ በክብርና በኃይል የምትበልጥ አንተ ነህ። 4 ይሁን እንጂ እንደ ውሃ የምትዋልል ስለሆንህ የበላይ አለቅነት ለአንተ አይገባም፣ ምክያንቱም የአባትህን መኝታ ደፍረሃል ምንጣፌንም አርክሰሃል። 5 “ስምዖንና ሌዊ ወንድማማቾች ናቸው፣ ዓመፅ ለመፈጸም የጦር መሣሪያዎቻቸውን ያነሳሉ። 6 ወደ ሸንጎአቸው አልግባ፣ ጉባኤያቸው ውስጥ አልገኝ፣ በቁጣ ተነሣስተው ወንዶችን ገድለዋል፣ የበሬዎችንም ቋንጃ እንደፈለጉ ቆራርጠዋል። 7 እጅግ አስፈሪ የሆነ ቁጣቸው፣ ጭከና የተሞላ ንዴታቸው የተረገመ ይሁን፤ በያዕቆብ እበትናቸዋለሁ፣ በመላው እስራኤልም አሠራጫቸዋለሁ። 8 ይሁዳ ወንድሞችህ ያመሰግኑሃል፣ እጅህም የጠላቶችህን አንገት አንቆ ይይዛል፣ የአባትህ ልጆች በፊትህ ተደፍተው ይስግዱልሃል። 9 ይሁዳ እንደ ደቦል አንበሳ ነው፣ ከዐደንህ የምትመለስ ልጄ፣ እንደ አንበሳ ያደፍጣል በምድርም ላይ ይተኛል፤ እንደ እንስት እንበሳም ያደባል፣ ታዲያ ማን ሊቀሰቅሰው ይደፍራል? 10 በትረ መንግስሥት ከይሁዳ እጅ አይወጣም፤ የገዥነት ምርኩዝም ከእግሮቹ መካከል፣ ሕዝቦች ሁሉ የሚታዘዙለት ‘ሴሎ’ እስኪመጣ ድረስ፣ ሕዝቦች ሁሉ ይታዘዙለታል። 11 አህያውን በወይን ግንድ፣ ውርንጫውንም በምርጡ የወይን ሐረግ ቅርንጫፍ ላይ ያስራል፣ ልብሱን በወይን ጠጅ፣ መጎናጸፊያውንም በወይን ጭማቂ ያጥባል። 12 ዓይኖቹ ከወይን ጠጅ የቀሉ፣ ጥርሶቹም ከወተት ይልቅ የነጡ ይሆናሉ። 13 ዛብሎን በባሕር ዳርቻ ይኖራል፣ የመርከቦቹ መጠጊያም ይሆናል፣ ወሰኑም እስከ ሲዶና ይደርሳል። 14 ይሳኮር፣ አጥንተ ብርቱ አህያ በጭነት መካከል የሚተኛ፣ ማረፊያ ቦታው መልካም፣ 15 ምድሪቱም አስደሳች መሆኗን ሲያይ፣ ትከሻውን ለሸክም ዝቅ ያደርጋል ከባድ የጉልበት ሥራም ይሠራል። 16 ዳን ከእስራኤል ነገዶች እንደ አንዱ ሆኖ በራሱ ሕዝብ ላይ ይፈርዳል። 17 ዳን የመንገድ ዳር እባብ፣ የመተላለፊያም መንገድ እፉኝት ነው፤ ጋላቢው የኋሊት እንዲወድቅ፣ የፈረሱን ሰኮና ይነክሳል። 18 እግዚአብሔር ሆይ፣ ማዳንህን እጠባበቃለሁ። 19 ጋድን ወራሪዎች አደጋ ይጥሉበታል፣ እርሱ ግን ዱካቸውን ተከታትሎ ብድሩን ይመልሳል። 20 አሴር ማዕደ ሰፊ ይሆናል፤ ለነገሥታትም የሚስማማ ምግብ ያቀርባል። 21 ነጻ እንደተለቀቀች ሚዳቋ ነው፣ የሚያማምሩ ግልገሎች ይኖሩታል። 22 ዮሴፍ፤ ፍሬያማ የወይን ተክል፣ በምንጭ ዳር የተተከለ ወይን ነው። ሐረጎቹ ቅጥርን ያለብሳሉ። 23 ቀስተኞች በብርቱ ያጠቁታል፤ በቀስታቸውም እየነደፉ ያሳድዱታል፤ 24 ነገር ግን በያዕቆብ ኃያል አምላክ ክንድ፣ እረኛም በሆነው በእስራኤል አለት ቀስቱ ጸና ጠንካራ ክንዱም ቀልጣፋ ሆነ። 25 አንተን በሚረዳህ በአባትህ አምላክ፣ በሚባርክህ ሁሉን በሚችል አምላክ፣ ከላይ ከሰማይ በሚገኝ ረድኤት፣ ከምድር ጥልቅ በሚገኝ በረከት፣ ከማኅፀንና ከጡት በሚገኝ ምርቃት ይባርክሃል። 26 ከጥንት ተራሮች በረከት፣ ከዘላለም ኮረብቶች ምርቃት ይልቅ፣ የአባትይ በረከት ይበልጣል፤ ይህ ሁሉ በዮሴፍ ራስ ላይ ይውረድ፤ በወንድሞቹ መካከል አለቃ በሆነውም ግንባር ላይ ይረፍ። 27 ብንያም ነጣቂ ተኩላ ነው፤ ያደነውን ማለዳ ይበላል፤ የማረከውን ማታ ያከፋፍላል። 28 እነዚህ ሁሉ ዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ናቸው። ይህም እያንዳንዳቸውን ተገቢ በሆነው በረከት አባታቸው ሲባርካቸው የተናገረው ቃል ነው። 29 ከዚህ በኋላ ያዕቆብ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፤ “እኔ የምሞትበትና ወደ ወገኖቼ የምሰበሰብበት ጊዜ ደርሶአል፤ ስለዚህ በኬጢያዊው በኤፍሮን እርሻ ውስጥ ባለችው ዋሻ ከአባቶቼ ዘንድ ቅበሩኝ፤ 30 ይህንን በከነዓን ምድር በመምሬ አጠገብ በማክፌል እርሻ ውስጥ ያለውን ዋሻ የመቃብር ቦታ እንዲሆን ከኬጢያዊው ኤፍሮን ላይ የገዛው አብርሃም ነው። 31 በዚያ አብርሃምና ሚስቱ ሣራ ተቀብረዋል፤ በዚያ ይስሐቅና ሚስቱ ርብቃ ተቀብረዋል፤ እኔም ልያን የቀበርኋት እዚያው ነው፤ 32 እርሻውና ዋሻው የተገዙት ከኬጢያውያን ላይ ነው።” 33 ያዕቆብ እነዚህን ቃላት ለልጆቹ ተናግሮ እንዳበቃ እግሮቹን በአልጋው ላይ ሰብስቦ የመጨረሻ ትንፋሹን ተንፍሶ ሞተ፣ ወደ ወገኖቹም ተሰበሰበ።



Genesis 49:1

አጠቃላይ መረጃ

ይህ ያዕቆብ ልጆቹን የሚባርከውን መጨረሻውን በረከት የጀምራል:: ይህም እስከ ዘፍጥረት 49:27 ይቀጥላል የያዕቆብ ምርቃቶች በግጥም መልክ ተጽፈዋል (ሥነ ግጥሞችን ይመልከቱ)

እናንተ የያዕቆብ ልጆች ሆይ ተሰብሰቡና ስሙ፤ አባታችሁ እስራኤልንም አድምጡ

ሁለቱ ዐረፍተ ነገሮች ትኩረት ለመስጠት ተመሣሣይ ሃሳብ ይናገራሉ አት ወደ አባታችሁ ኑና በጥንቃቄ አድምጡ (ተመሣሣይ ተነጻጻሪ ይመልከቱ)

እናንተ የያዕቆብ ልጆች አባታችሁን እስራኤልን አድምጡ

ያዕቆብ ራሱን እንደሶስተኛ ወገን ሰው ያቀርባል እንደአንደኛ ወገን ሰው ሊገለጽ ይችላል አት ልጆች ሆይ እኔን አባታችሁን ስሙ (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አጠቃቀም ይመልከቱ)

Genesis 49:3

የበኩር ልጄ ኃይሌና የጉብዝናዬ መጀመሪያ

የበኩር ልጄ ኃይሌ የጉብዝናዬ መጀመሪያ የሚሉ ሀረጐች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው ኃይል እና ጉብዝና የሚሉ ቃሎች የያዕቆብ ልጅ የመውለድ አቅሙን ያመለክታሉ በኩር እና መጀመሪያ የሚሉ ቃላት ሮቤል በኩር ልጁ እንደሆነ ይገልጻሉ (ተመሣሣይ ተነጻጻሪ ይመልከቱ)

በክብር ትልቃለህ በኃይልም ትበልጣለህ

ይህ እንደ አድስ ዐረፍተ ነገር ሊገለጽ ይችላል አት በክብርና በኃይል የመጀመሪያ ትሆናለህ ወይም በክብርና በኃይል ማንኛውንም ሰው ትበልጣለህ

እንደ ውሃ የምትዋልል ነህ

ያዕቆብ ሮቤል ቁጣውን እንደማይችል ለማተኮር በከባድ ማዕበል እንደሚዋልል ውሃ አድርጐ ያቀርበዋልና እርሱ የተረጋጋ አይደለም (ተመሣሣይ አባባል ይመልከቱ)

እልቅና አይኖርህም

በወንድሞችህ መካከል የመጀመሪያ ወይም አለቃ አትሆንም

ወደ አባትህ መኝታ ወጥተሃልና ከዚያም አርክሰሄዋል ወደ አልጋዬም ወጥተሃል

እዚህ መኝታና አልጋ የያዕቆብን ቁባት ባላን ያመለክታሉ ያዕቆብ ሮቤል ከባላ ጋር የተኛበትን ያመለክታል (ዘፍጥረት 35:22 ይመልከቱ) አት “ወደ አልጋዬ ስለወጣህና በቁባቴ ከባላ ጋር ስለተኛህ አዋርደህኛልና” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

ወደ አባትህ አልጋ ወጥተሃል ወደ አልጋዬም ወጥተሃል

ሁለቱም ዐረፍተ ነገሮች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው (ተመሣሣይ ተነጻጻሪ ይመልከቱ)

Genesis 49:5

ስምዖንና ሌዊ ወንድማማቾች ናቸው

ይህ በትውልድ ወንድሞች መሆናቸውን አይገልጽም ያዕቆብ የሴኬም ሰዎችን ለመግደል አብረው መሥራታቸውን ለማተኮር ነው፡፡

ሰይፎቻቸው የዐመጽ መሣሪያ ናቸው

ሰዎችን ለመጉዳትና ለመግደል ሰይፎቻቸውን ይጠቀማሉ

ነፍሴ …. ልቤ

ያዕቆብ ራሱን ለመግለጽ ነፍሴ እና ልቤ የሚሉ ቃሎችን ይጠቀማልና ክፋን ለማድረግ ከሚያቅዱት ጋር ባለመተባበሩ ሌሎች ሰዎችና እግዚአብሔርም ደግሞ እጅግ እንዳከበሩት ይናገራል (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ወደ ሸንጐአቸው አልግባ

ጉባዔያቸው ውስጥ አልገኝ እነዚህ ሁለቱ ሀረጐች በመሠረቱ ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው ያዕቆብ ሁለቱን በማገናኘት በክፉ እቅዳቸው እንደማይሳተፍ አበክሮ ይገልጻል አት ማንኛውንም እቅድ ለማዘጋጀት ከእነርሱ ጋር አልተባበርም (ተመሣሣይ ተነጻጻሪ ይመልከቱ)

የቤሬዎችን ቋንጃ ቈራርጠዋል

ስምዖንና ለዊ ለዕይታ ብለው ቤሬዎችን አስነክሰዋል

ቋንጃ መቈረጥ ወይም ማስነከስ

ይህ የእንስሳትን ቋንጃ በመቁረጥ እንዳይራመዱ ማድረግ ነው

Genesis 49:7

ቁጣቸው ርጉም ይሁን ጽኑ ነበርና ንዴታቸው ጭከና የተሞላ ነበርና

እግዚአብሔር ስምዖንና ሌዊን የሚረግመው እግዚአብሔር ቁጣቸውንና ንዴታቸውን እንደሚረግም ተደርጐ የገልጾአል:: (ዘይቤያዊ አነጋገርና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ቁጣቸው የተረገመ ይሁን

አብዛኛውን ጊዜ ነብይ ትንቢትን ሲናገር የሚናገረው ቃል እግዚአብሔር እንደሚናገር ይቆጠራል:: ይህም የሚናገረው ነበዩና እግዚአብሔር እንዴት እንደተቆራኙ ነው::

ንዴታቸው ጭከና የተሞላ ስለነበር

እረግማለሁ የሚለው ቃል የታወቀ ነው አት ንዴታቸው ጭከናን የተሞላ ስለሆነ እረግማለሁ (የተደበቁትን የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

እኔም በያዕቆብ እከፋፍላቸዋለሁ በእስራእልም እበትናቸዋለሁ

“እኔ” እግዚአብሔርን ያመለክታል:: “እነርሱ” ስምዖንንና ለዊን ቢሆንም ምትክ ቃል ስለሆነ ለትውልዳቸውም ይሆናል:: “ያዕቆብ”ና “እስራኤል” ተወራራሽ ስሞችና የእስራእል ሕዝብ የሚተኩ ናቸው:: አት ትውልዳቸውን እበትናለሁ በእስራኤልም ሰዎች መካከል አሠራጫለሁ (ምትክ ቃላትና ተመሣሣይ ተነጻጻሪ አባባል ይመልከቱ)

Genesis 49:8

ወንድሞችህ አንተን ያመሰግኑሃል የአባትህ ልጆች በፊትህ ይሰግዳሉ

ሁለቱም ዐረፍተ ነገሮች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው (ተመሣሣይ ተነጻጻሪ ይመልከቱ)

ያመሰግኑሃል፤ እጅህ

ሁለተኛው ዐረፍተ ነገር ለአንደኛው ምክንያት ነው ይህ “ስለ” ወይም “ምክንያቱም/የተነሣ” አገናኝ ቃላትን በመጠቀም ግልጽ ሊሆን ይችላል:: አት “ስለ እጅህ ያመሰግኑሃል” ወይም “ከእጅህ የተነሣ ያመሠግኑሃል” (አገናኝ ቃላት ይመልከቱ)

እጅህ በጠላቶችህ አንገት ላይ ነው

“ጠላቶችህን ታሸንፋለህ” የሚል አባባል ነው:: (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ይሰግዳሉ

ለአንድ ሰው እጅ መንሣት ወይም አክብሮት በትህትና ለመግለጽ ጐንበስ ማለትን ይገልጻል (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Genesis 49:9

ይሁዳ የአንበሳ ደቦል ነው

የአንበባ ደቦል እንደሆነ ስለ ይሁዳ ያዕቆብ ይናገራል:: ያዕቆብ የይሁዳን ጥንካሬ በአትኩሮት ይገልጻል:: አት “ይሁዳ እንደ አንበሳ ደቦል ነው” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ልጄ ሆይ ከአደንህ ወጣህ

“አንተ ልጄ ከአደንህ ተመለስህ”

እንደ እንስት አንበሳ

ያዕቆብ ይሁዳን ከእንስት አንበሳ ጋር ያነጻጽራል አት እንስት አንበሳ በአደን ቀዳማይና ቡድንዋን የሚትከላከል ነች (ተመሣሣይ አባባል ይመልከቱ)

ያስነሣውስ ዘንድ ማን ይችላል?

ያዕቆብ ይሁዳ ለሌሎች ሰዎች ምንኛ አስፈሪ እንደሆነ ትኩረት ለመሰጠቅ ጥያቄ ይጠቀማል፡፡ አት “ማንም ሊቀሰቅሰው አይችልም” (አግናኝ ጥያቄ ይመልከቱ)

Genesis 49:10

በትሬ መንግሥት ከይሁዳ አይጠፋም የገዥም ዘንግ ከእግሮቹ መካከል

በትርና ዘንግ ንጉሥ የሚይዛቸው ያገጡ ረጃጅም በትሮች ናቸው የሥልጣን አገዛዝ የሚተኩ ምልክቶች ናቸው እናም ይሁዳ የእርሱን ዘር ይወክላል:: አት “የአገዛዝ ሥልጣን ሁልጊዜም ለይሁዳ ዘር ይሆናል” (ምትክ ቃላትና ተመሣሣይ ተነጻጻሪ አባባል ይመልከቱ)

ገዥነት የሚገባው ወይም ሰሎ እስኪመጣ ድረስ

ተገቢ ትርጉሞች 1 ሰሎ ማለት ክብር ወይም አድናቆት ማለት ነው አት ሕዝቦች እስኪታዘዙለትና እስክያከብሩት ድረስ ወይም 2 ሰሎ የሴሎ ከተማን ይወክላል አት ገዥ ወደ ሰሎ እስኪመጣና ሕዝቦች እስኪታዘዙለት ድረስ ብዙ ሰዎች እንደሚናገሩት ይህ ትንቢት ከዳዊት ዘር ስለሚመጣው መስህ ነው ዳዊት ከይሁዳ ዘር ነውና

ሕዝቦች ይታዘዙለታል

ሕዝቦች ሰዎችን ያመለክታሉ አት ሕዝቦች ሁሉ ይታዘዙለታል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

Genesis 49:11

አህያውን ያስራል… በወይን ግንድ

ሁለቱም አረፍተ ነገሮች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው የወይኑ ፍሬ ብዙ ሰለሆነ አህያው ፍሬዎችን ቢበላ ጌታው እንደማይገደው ተደረጐ ተገልጾአል:: (ተመሣሣይ ተነጻጻሪ እና ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የእርሱ … እርሱ

የእርሱ ወይም እርሱ በተጠቀሱባቸው ሁሉ ተገቢ ትርጉማቸው 1 የይሁዳን ዘር ያመለክታሉ:: “የእነርሱ” “እነርሱ” ወይም 2) እነርሱ በዘፍጥረት 49:1ዐ ምናልባት ሚናሴን የሚያመለክተውን ገዥ ያመለክታሉ::

ልበሱን ያጥባል… በወይን ጭማቂ

ሁለቱም ዐረፍተ ነገሮች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው ይህም በጭማቂዎቻቸው ልብሶቻቸውን ማጠብ እንኳ የሚያስችል ብዙ ወይን ፍሬዎች ይኖራሉ ማለት ነው (ተመሣሣይ ተነጻጻሪ እና ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አጠበ

አብዛኛውን ጊዜ ወደፊት የሚፈጸሙ ትንብቶች እንደተፈጸመ ተደርጐ ይገለጻል ይህ በአትኩሮት የሚናገረው ክስተቱ በእርግጥ እንደሚፈጸም ነው አት እነርሱ ያጥባሉ ወይም እርሱ ያጥባል (ወደፊት አመላካች ኃላፊ ክስተት ይመልከቱ)

የወይን ደም ወይም ጭማቂ

የወይን ጭማቂን እንደ ወይን ደም ያቀርባል ይህም ጭማቂው ምንኛ ቀይ ቀለም እንዳለው ይገልጻል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ዐይኖቹ እንደ ወይን የቀሉ

ይህ እንደ ቀይ ቀለም ወይን የሰውን ዐይን ቀለም ቅላት ያመለክታል:: ተገቡ አማራጭ ትርጉሞች እነሆ አት 1)ጥቁር ቀለም ያላቸው ዐይኖች ጤናማ ዐይኖች ናቸው ወይም 2) ብዙ የወይን ጠጅ ከመጠጣት የተነሣ የሰዎች ዐይኖች ይቀላሉ (ተመሣሣይ አባባል እና ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ጥርሶቹ ከወተት ይልቅ የነጡ

ይህ የሰውን ነጭ ጥርስ ከወተት ንጣት ጋር ያነጻጽራል፡፡ ይህም ወተትን የሚጠጡበት ብዙ የሚታለቡ ላሞች እንደሚኖሩ ነው (ተመሣሣይ አባባል እና ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Genesis 49:13

ዛብሎን በበሕር ዳር ይኖራል

ይህ የዛብሎንን ነገድ ያመለክታል:: የዛብሎት ነገድ ወይም ትውልድ በበሕር ዳር ይኖራል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

እርሱም ወደብ ይሆናል

እዚህ እርሱ የዛብሎን ሰዎች የሚወርሱት ወይም የሚገነቡት የባሕር ዳር ከተሞችን ይወክላል እነዚህ የወደብ ከተሞች ለመረከበኞች መጠለያ ይሆናሉ (ምትክ ቃል አጠቃቀም ይመልከቱ)

ወደብ

በባህር ዳር ያለ መሬትና ለመርከቦች መቆሚያ ደኀንነት ያለው ቦታ ማለት ነው

Genesis 49:14

ይሳኮር አጥንተ ብርቱ አህያ ነው

ያዕቆብ ስለይሳኮርና ነገድ ወይም ትውልድ ሲናገር እንደ አህያ ይቆጥራቸዋል ይህም እጅግ የሚሠሩ እንደሚሆኑ በአትኩሮት ይገልጻል የይሳኮር ትውልድ አንደ አጥንተ ብርቱ አህያ ነው (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ይሳኮርም

አብዛኛውን ጊዜ ወደፊት የሚፈጸሙ ትንቢቶች እንደተፈጸመ ተደርጐ ይገለጻል ይህ በአትኩሮት የሚናገረው ክስተቱ በእርግጥ እንደሚፈጸም ነው ይህም በወደፊት ጊዜ ሊገለጽ ይችላል አት “ይሳኮር… ይሆናል” ወይም “የይሳኮር ትውልድ… ይሆናል” (ወደፊት አመላካች ኃላፊ ክስተት ይመልከቱ)

ይሳኮር …ያያል… ይሆናል

እዚህ ይሳኮር ለነገዱ ምትክ ሆኖ የሚቆም ስም ነው አት “የይሳኮር ትውልዶች… ያያሉ …ይሆናሉ” (ምትክ ቃላት ይጠቀሙ)

በበጐች ጉሬኖ መካከል ያርፋል

ተገቢ ትርጉሞች 1 በጭነት መካከል ይተኛል ወይም 2 በሁለት በጐች አጥር መካከል ይተኛል ደግሞም በሌላ መንገድ ያዕቆብ ስለይሳኮር ልጆች እጅግ እንደሚሠሩና ከዚያም ለእረፍት እንደሚተኙ ይናገራል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

መልካም የእረፍት ቦታና የለማች ምድር

መልካም እረፍት የሚያገኙበት ቦታና የለማች ምድር

ትከሻውን ለሸክም ያመቻቻል

ትከሻውን ለሽክም ያመቻቻል ማለት ሸክምን በመሸከም እጅግ ይሠራል ማለት ነው (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ለሥራ ባሪያ ይሆናል

ለሌሎች እንደባሪያ ያገለግላል

Genesis 49:16

ዳን በወገኑ ይፈርዳል

እዚህ ዳን ነገዱን ይወክላል የዳን ልጆች በራሱ ሕዝብ ላይ ይፈርዳል ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ

የራሱ ሕዝብ

ተገቢ ትርጉሞች የራሱ ሕዝብ፤ 1) በዳን ሕዝብ 2) በእስራኤል ሕዝብ

ዳን የመንገድ ዳር እባብ ይሆናል

ያዕቆብ ስለዳንና የእርሱ ትውልድ እንደ እባብ አድርጐ ይናገራቸዋል እባብ ምንም ትንሽ ቢሆን መንገደኛውን ከፈረስ ላይ ማውረድ ይችላል እንዲሁ ዳን ትንሽ ነገድ ሲሆን በጠላቶቹ ላይ አደገኛ ነው አት የዳን ልጆች በመንገድ ዳር እንዳለ እባብ ናቸው (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ሆይ ማዳንህን እጠባበቃለሁ

ረቂቅ ስም “ማዳን” እንደ “መዳን” ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት “እግዚአብሔር ሆይ እንዲታድነኝ እጠባብቃለሁ”

እኔ እጠባበቃለሁ

“እኔ” ያዕቆብን ያመለክታል

Genesis 49:19

ጋድ …ይዘምቱበታል እርሱ ግን

ጋድ ትውልዱን ይወክላል:: አት “የጋድ ልጆች ..ይጠቃሉ ነገር ግን እነርሱ” (ምትክ ቃል ይጠቀሙ)

አሴር ማእደ ሰፊ ይሆናል …እርሱም

አሴር የአሴር ልጆችን ይወክላል:: እት “የአሴር ልጆች ማእደ ሰፊ… እናም እነርሱ” ምትክ ቃል ይጠቀሙ

ንፍታሌም …እርሱም

ንፍታሌም የንፍታሌምን ትውልድ ይወክላል:: አት “የንፍታሌም ልጆች.. እነርሱ… ይሆናሉ”

በተራሮች

ከዳን ልጆች በመሸሽ በተራራማው የሚኖሩ ሰዎችን ያመለክታል

ምግቡ የተረከተ

እዚህ የበረከተ የሚለው ምግቡ ጣፋጭ ማለት ነው ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ

ንፍታለም ነጻ እንደተለቀቀች ሚዳቋ ነው

ያዕቆብ ስለንፍታሌም ልጆች ለመሮጥ እንደተለቀቀች እንደ እንስት ሚዳቋ እንደሆነ ይናገራል:: ይህም እነርሱ ፈጣን መልእክተኞች እንደሆኑ ነው:: አት “የንፍታሌም ዘሮች እንደተለቀቀች ሚዳቋ ይሆናሉ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የሚያማምሩ ግልገሎች

ግልገሎች ትናንሽ የሚዳቋ ግልገሎች ናቸው የዕብራይስጡ ቃል ትርጉም ግልጽ አይደለም አንዳንድ ትርጉሞች መልካም ቃል ይሰጣል ወይም መልካም ነገር ይናገራል የሚለውን ተጠቅመዋል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 49:22

ዮሴፍ ፍሬያማ ዛፍ ነው

ዮሴፍ ትውልዱን/ዘሩን ይወክላል ያዕቆብ እነርሱን ብዙ ፍሬ እንደሚያፈራ የዛፍ ቅርንጫፍ አድርጐ ይናገራል:: አት “የዮሴፍ ዘር ፍሬያማ የዛፍ ቅርንጫፍ ነው”

የዛፍ ቅርንጫፍ

የዛፍ ዋና ቅርንጫፍ

ሐረጐቹ ቅጥርን ያለብሳሉ

ቅርንጫፎች አድገው ቅጥርን ማልበሳቸው እነዚያ በቅጥር ላይ እንደሚወጡ ተደርጐ ተገልጾአል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 49:24

አጠቃላይ መረጃ

ያዕቆብ ዮሴፍንና ዘሩን መባረክ ይቀጥላል

ቀስቱ ጸና

ቀስቱን የያዘው ሰው መጽናቱ ቀስቱ ራሱ እንደጸና ተደርጐ ተግልጾአል ወደ ጠላቱ በሚያልምበት ጊዜ ቀስቱ እንደሚጸና ይገልጻል አት ወደ ጠላቱ በሚያልምበት ጊዜ ቀስቱን አጽንቶ ይይዛል (ምትክ ቃላት አጠቃቀም እና ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ቀስቱ….እጆቹ

እዚህ “እርሱ” ዘሩን የሚወክለውን ዮሴፍን ነው አት “ቀስቶቻቸውና እጆቻቸው” (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

እጆቹ ቀልጣፋ ይሆናሉ

ቀስትን መያዘ የለመዱ እጆች ስለሆኑ ሙሉ ሰው እንደ እጆች ተገልጾአል:: (ክፍልን እንደሙሉና ሙሉን እንደክፍል የመግልጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ኃያል አምላክ እጆች

እጆች የእግዚአብሔርን ኃይል ይገልጻሉ:: አት “የሁሉን ቻይ አምላክ ኃይል” (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

ከእረኛው ስም የተነሣ

እዚህ ስም ሙሉ ሰው ይወክላል አት ከእረኛው የተነሣ (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

እረኛው

ያዕቆብ እግዚአብሔር እረኛ እንደሆነ ይናገራል አት ይህም እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደሚመራና እንደሚጠብቅ ይናገራል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ዐለት

ያዕቆብ እግዚአብሔር ሰዎች የሚወጡበትና ከጠላቶቻቸው የምድኑበት አለት እንደሆነ ይናገራል ይህ የሚያጐላው እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደሚጠብቅ ነው (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 49:25

አጠቃላይ መረጃ

ያዕቆብ ዮሴፍንና ዘሩን መባረክ ይቀጥላል (ዘፍጥረት 49:22-23 ይመልከቱ)

አንተን በሚረዳህ …በሚባርክህ

እዚህ “አንተ” ዘሩን የሚወክለውን ዮሴፍን ያመለክታል አት “የአንተን ዘር በሚረዳ ….በሚባርክህ” (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

በሰማይ በረከቶች

ሰማይ ተክልን ወይም ሰብልን የሚያሳድገው ዝናብን ይወክላል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

ከምድር ጥልቅ ከሚገኝ በረከት

ጥልቅ ለወንዞችና ለኩሬዎች የሚሆን ውሃ የሚወጣበትን ይወክላል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

በጡትና በማህጸን በረከት

እዚህ ጡቶችና ማህጸን እናቶች የመውለድና ጡት የማጥባት አቅም ያመለክታል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

Genesis 49:26

አጠቃላይ መረጃ

ያዕቆብ ዮሴፍንና ልጆቹን መባረክ ይቀጥላል፡፡

ከጥንት ተራሮች

የመሠረታዊው ቋንቋ ትርጉም ግልጽ አይደለም:: አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች በጥንት ተራሮች ፈንታ ጥንት አባቶች ይጠቀማሉ::

እነርሱ በዮሴፍ ራስ ላይ ይሁኑ

እዚህ “እነርሱ” የአባቱ በረከቶች ናቸው::

በወንድሞች መካከል አለቃ በሆነው ራስ አናት ላይ

ያዕቆብ እነዚህ በረከቶች ልጆቹ እጅግ በበለጡት ላይ እንዲሆን ይሻል:: አት “እጅግ በበለጡ በዮሴፍ ልጆች ራስ አናት ላይ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በወንድሞቹ መካከል አለቃ በሆነው

ከወንድሞቹ ዋና በሆነው

Genesis 49:27

ብንያም ነጣቂ ተኩላ ነው

ብንያም ዘሩን የሚወክል ምትክ ስም ነው:: ያዕቆብ የብያም ልጆችን እንደ ተራበ ተኩላ ይናገራል:: ይህም አጉልቶ የሚናገረው አጥቂ ተዋጊዎች እንደሆኑ ነው:: የብንያም ነገድ ሰዎች እንደተራቡ ተኩላ ናቸው:: (ምትክ ቃልና ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 49:28

እነዚህ አሥራ ሁሉቱ የእስራኤል ነገዶች ናቸው

እነዚህም በዘፍጥረት 49: 1- 27 የተዘረዘሩትን ይመለከታል እያንዳንዱ ልጅ የነገድ አባት ሆኖአል፡፡

በባረካቸው ጊዜ

እዚህ “ባረካቸው” የሚለው መደበኛ በረከቶችን እንደተናገረ ነው

እያንዳንዱን በተገቢ መንገድ ባረካቸው

ለእያንዳንዱ የሚገባውን በረከት ባረከ

መመሪያ ሰጣቸው

አዘዛቸው

ወደ ወገኖቼ የምሄድበት ጊዜ ደርሶአል

ይህ ለመሞት መድረሱን በትህትና የሚገለጸበት መንገድ ነው፡፡ አት “ለመሞት ቀርበአለሁ ወይም ልሞት ነኝ” (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ መንገድ መግለጽንና ፈሊጣዊ አነጋገርን ይመልከቱ)

ወደ ወገኖቼ የምሄድበት

ያዕቆብ በሚሞትበት ጊዜ የራሱ ውስጠኛው ሰው/ ነፍሱ ወደየት እንደሚሄድ ያመለክታል:: ከሞት በኋላ አብርሃምንና ይስሐቅን አንደሚገናኝ ይጠብቃል (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ መንገድ መግለጽንና ፈሊጣዊ አነጋገርን ይመልከቱ)

ኬጢያዊው ኤፍሮን

ይህ ወንድ ሰው ስም ነው፡፡ “ኬጢያዊ” የኬጥ ዘር ነው:: በዘፍጥረት 23:8 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ማክፌላ

የአንድ ቦታ ወይም ግዛት ስም ነው፡፡ በዘፍጥረት 23፡9 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

መምሬ

ይህ የሔብሮን ከተማ ሌላ ስምዋ ነው:: ምናልባት መምሬ የተባለው የአብርሃም ወዳጅ ስም የተሰየመ ሳይሆን አይቀርም:: በዘፍጥረት 13:18 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ(ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 49:31

አጠቃላይ መረጃ

ያዕቆብ ለልጆቹ መናገሩን ይቀጥላል

በዚያ የተገዛው

ግዥው ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት “በዚያ አብርሃም የገዛውን” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ከኬጥ ሰዎች

ከኬጢያዊያን

እነዚህን መመሪያዎች ለልጆች ተናግሮ እንዳበቃ

“ለልጆቹ መመሪያ መሰጠቱን እንዳበቃ” ወይም “ልጆቹን አዝዞ እንዳበቃ”

እግሮቹን በአልጋው ላይ ሰብስቦ

ያዕቆብ በአልጋው ላይ ተቀምጦ ነበር አሁን ግን ሊሞት መልሶ እግሮቹን በአልጋ ላይ የሰበስባል

የመጨረሻ አስትንፋሱን ተነፈሰ/ሰጠ

ይህ አንድ ሰው መሞቱን ለዛ ባለ ቋንቋ የሚገለጽበት መንገድ ነው (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ መንገድ መግለጽን ይመልከቱ)

ወደ ወገኖቹ ተሰበሰበ

ያዕቆብ በሞተ ጊዜ ውስጠኛው ሰው ወይም ነፍሱ ከእርሱ በፊት የሞቱ ወገኖች ወደሄዱበት ቦታ ተሰብስቦአል (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ መንገድ መግለጽንና ፈሊጣዊ አነጋገርን ይመልከቱ)


Chapter 50

1 ዮሴፍ እጅግ ከማዘኑ የተነሣ በአባቱ ፊት ተደፍቶ አለቀሰ ሳመውም። 2 ከዚያም የአባቱ የእስራኤል አስከሬን እንዳይፈርስ ባለ መድኃኒት የሆኑ አገለጋዮች በመድኃኒት እንዲያሹት አዘዘ። ባለ መድኃኒቶቹም አስከሬኑ እንዳይፈርስ በመድኃኒት አሹት። 3 በአገሩ ልማድ መሠረት አስከሬኑ እንዳይፈርስ ማሸቱ አርባ ቀን ወሰደባቸው፤ ገብፃውያንም ሰባ ቀን አለቀሱለት። 4 የለቅሶው ወራት በተፈጸመ ጊዜ ዮሴፍ የፈርዖንን ባለሥልጣኖች እንዲህ አላቸው፤ “መልካም ፈቃዳችሁ ቢሆን እባካችሁ ለፈርዖን፣ 5 ‘አባቴ ለመሞት ሲቃረብ በከነዓን ምድር ባዘጋጀው መቃብር እንድቀብረው በመሐላ ቃል አስገብቶኛል፤ ስለዚህ ወደዚያ ሄጄ አባቴን ቀብሬ እንድመለስ ይፈቀድልኝ ሲል ጠይቆአል’ ብላችሁ ንገሩልኝ” አላቸው። 6 ፈርዖንም፣ “ባስማለህ መሠረት ሄደህ አባትህን ቅበር” አለው። 7 ስለዚህ ዮሴፍ አባቱን ለመቅበር ሄደ፣ የፈርዖን ሹማምንት በሙሉ፣ የቤተ መንግሥቱ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች እንዲሁም የግብፅ ከፍተኛ ባለ ሥልጣኖች ሁሉ ተከተሉት። 8 እንደዚሁም የዮሴፍ ቤተ ሰቦች ወንድሞቹና ሌሎችም የአባቱ ቤተ ሰቦች ሁሉ ከዮሴር ጋር ሄዱ፣ በጌሤም የቀሩት ሕፃናት ልጆቻቸው፣ የበግ፣ የፍየልና የከብት መንጋዎቻቸው ብቻ ነበሩ። 9 እንዲሁም ሠረገሎች፣ ፈረሰኞች አብረውት ወጡ፤ አጀቡም እጅግ ብዙ ነበር። 10 እነርሱም በዮርዳኖስ ማዶ ካለው አጣድ ከተባለው ዐውድማ ሲደርሱ ድምፃቸውን ከፍ በማድረግ ምርር ብለው አለቀሱ፤ ዮሴፍም በዚያ ለአባቱ ሰባት ቀን ለቅሶ ተቀመጠ። 11 በዚያ የሚኖሩ ከነዓናውያን በአጣድ ዐውድማ የተደረገውን ልቅሶ ባዩ ጊዜ፣ “ይህ ለግብፃውያን መራራ ልቅሶአቸው ነው” አሉ። በዮርዳኖስ አጠገብ ያለው የዚያ ቦታ ስም አቤል ምጽራይም ተብሎ መጠራቱም ከዚሁ የተነሣ ነበር። 12 በዚህ ሁኔታ የያዕቆብ ልጆች አባታቸው እንዳዘዛቸው አደረጉ፤ 13 አስከሬኑን ወደ ከነዓን ወስደው ከመምሬ በስተምሥራቅ በምትገኘው በማክፌላ ዋሻ ቀበሩት፤ ይህም ዋሻ አብርሃም ለመቃብር ቦት እንዲሆን ከኬጢያዊው ከኤፍሮን በገዛው እርሻ ውስጥ የሚገኝ ነው። 14 ዮሴፍ አባቱን ከቀበረ በኋላ ከወንድሞቹና ለቀብር አጅበውት ከሄዱት ሰዎች ሁሉ ጋር ሆኖ ወደ ግብፅ ተመለሰ። 15 የዮሴፍ ወንድሞች ከአባታቸው ሞት በኋላ፣ “ከፈጸምንበት በደል የተነሣ ዮሴፍ ቂም ይዞ በበቀልን ምን እናደርጋለን ተባባሉ። 16 ስለዚህ እንዲህ የሚል መልእክት ላኩ፣ አባትህ ከመሞቱ በፊት፣ 17 ‘ለዮሴፍ ወንድሞችህ በአንተ ላይ የፈጸሙትን ኃጢአትና ክፉ በደል ይቅር በላቸው’ ብላችሁ ንገሩት የሚል ትእዛዝ አስተላልፎ ነበር። አሁንም የአባትህን አምላክ አገልጋዮች ኃጢአት ይቅር በለን።” ዮሴፍ ይህን በሰማ ጊዜ አለቀሰ። 18 ከዚያም ወንድሞቹ መጡና በፊቱ ተደፍተው፣ “እኛ የአንተ አገልጋዮች ነን” አሉት። 19 ዮሴፍ ግን እንዲህ አላቸው፤ “አትፍሩ፣ እኔ በእግዚአብሔር ምትክ የተቀመጥሁ አይደለሁም፣ 20 እናንተ እኔን ለመጉዳት አስባችሁ አድርጋችሁት ነበር፤ እግዚአብሔር ግን ዛሬ እንደሚታየው ሁሉ የብዙዎችን ሕይወት ለማዳን ለበጎ ነገር አዋለው። 21 አሁንም ቢሆን አትፍሩ፤ ለእናንተና ለልጆቻችሁ የሚያስፈልጋችሁን ሁሉ አደርግላችኋለሁ” በማለት በመልካም ንግግር አረጋጋቸው። 22 ዮሴፍ ከአባቱ ቤተ ሰቦች ጋር በግብፅ ተቀመጠ፤ አንድ መቶ ዐሥር ዓመትም ኖረ፤ 23 የኤፍሬምንም የልጅ ልጆች እስከ ሦስት ትውልድ ድረስ ዐየ። ከምናሴ የተወለደውንም የማኪርንም ልጆች በጭኑ ላይ አድርጎ አቀፋቸው። 24 ከዚህ በኋላ ዮሴፍ ወንድሞቹን እንዲህ አላቸው፤ “እነሆ፣ እኔ የምሞትበት ጊዜ ተቃርቦአል፤ እናንተ ግን እግዚአብሔር በረድኤት ይጎበኛችኋል፤ ከዚህም አገር አውጥቶ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ለመስጠት በመሐላ ቃል ወደገባላቸው ምድር ይመልሳችኋል። 25 እግዚአብሔር በሚጎበኛችሁና ወደዚያች ምድር በሚመልሳችሁ ጊዜ ዐጽሜን ከዚህ ይዛችሁ የምትወጡ መሆናችሁን በማረጋገጥ ቃል ግቡልኝ” ብሎ አስማላቸው። 26 ዮሴፍም ዕድሜው መቶ ዐሥር ዓመት ሲሞላው ሞተ፣ አስከሬኑንም መድኃኒት ቀብተው በሬሳ ሳጥን ካስገቡት በኋላ በግብፅ ምድር አስቀመጡት።



Genesis 50:1

በአባቱ ፊት ተደፍቶ

እዚህ ተደፍቶ የሚለው ፈሊጣዊ አባባል ተመስጦ ማለት ነው፡፡ አት “በአባቱ ላይ ተደፍቶ በሀዘን” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ባለመድኃኒት የሆኑ አገልጋዮቹ

አስከሬንን የሚያስተካክሉ አገልጋዮቹ

የአባቱን አስከሬን እንዲቀቡት

መቀባት ከቀብር በፊት አስከሬኑ እንዳይፈርስ የሚያቆዩበት ልዩ መንገድ ነው (ንኀብነት ወይም ለዛ ባለ መንገድ መግለጽን ይመልከቱ)

አርባ ቀን ወሰደባቸው

4ዐ ቀናት ወሰደባቸው (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ሰባ ቀናት

7ዐ ቀናት (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

Genesis 50:4

የሐዘኑ ጊዜ እንዳበቃ

“የማዘኑ ቀናት” ወይም “ለእርሱ የማልቀስ ቀናት”

ዮሴፍ ለፈርዖን ቤት ተናገረ

እዚህ የፈርዖን ቤት የፈርዖን ንጉሣዊ ፍርድ ቤት ወክል ባለሥልጣናት ያመለክታል ዮሴፍ ለፈርዖን ባለሥልጣናት ተናገረ (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

በፊታችሁ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ

ሞገስ ማግኘት የሚለው ሐረግ በአንድ ሰው ፊት ተቀባይነትን ማትረፍ የሚናገር ፈሊጣዊ አባባል ነው:: አት “በእናንተ ፊት ሞገስ ካገኘሁ ወይም በእኔ ደስተኞች ከሆናችሁ” (ፈሊጣዊ አባባልና ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ለፈርዖን እንዲህ ብላችሁ ንገሩልኝ ፤አባቴ አምሎኛል፤ እንዲህ ስል፤ እነሆ እኔ እሞታለሁ፤ በቆፈርሁትም መቃብር በከነዓን ምድር ከዚያ ቅበረኝ ፡፡ አሁንም ወጥቼ አባቴን ሊቅበርና ሊመለስ፡፡

ይህ ሁለት ደረጃና ሶስት ደረጃ ጥቅስ ይዞአል እነዚህ በተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጹ ይችላሉ:: አት “በከነዓን ምድር በቆፈረው መቃብር እንዲቀብረው አባቴ በሚሞትበት ጊዜ እንዳመለኝ ለፈርዖን ንገሩልኝ:: አባተን እንዲቀብረውና ከዚያም ተመልሸ እንዲመጣ ፈርዖንን ጠይቁልኝ” (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

እኔ ልሞት ቀርበአለሁ

ሊሞት ነኝ

ልውጣ

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደ ላይ መውጣት” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነው፡፡

ፈርዖንም መለሰ

የመንግሥት ምክር ቤት አባላት ለፈርዖን ነገሩትና ከዚያም ፈርዖን ለዮሴፍ መለሰ (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

አባትህ እንዳማለህ

ለእርሱ እንደማልህለት

Genesis 50:7

ዮሴፍም… ወጣ

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደ ላይ መውጣት” የሚለውን ሀረግ መጠቀም የተለመደ ነው፡፡

የፈርዖን ሹማምንት በሙሉ የቤቱ ሽማግሌዎች/የቤተመንግሥቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናትና የግብጽ ምድር ከፍተኛ ባለሥልጣናት

የፈርዖን ከፍተኛ መሪዎች ሁሉ የቀብሩን ሥነሥርዓት ተካፈሉ (የሁኔቶች ሥርዓት ይመልከቱ)

የቤቱ ሽማግሌዎች

የፈሪዖን ቤተምንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናትን ያመለክታል

ከግብጽ ምድር ፤የዮሴፍ ቤተ ሰዎች ወንድሞቹና የአባቱ ቤተ ሰዎች

ይህ እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ሊተረጐም ይችላል:: አት “የግብጽ ምድር ፤ እንዲሁም የዮሴፍ ቤተ ሰዎች ወንድሞቹና የአባቱ ቤተ ሰዎች ከእርሱ ጋር አብረውት ሄዱ” (የሁኔቶች ቅደም ተከተል ይመልከቱ)

ሰረገላዎች

እዚህ በሠረገላዎች የተቀመጡ ሰዎችን ያመለክታል (ምትክ ቃላት ይመልከቱ)

እጅግ ብዙ ሰዎች ነበሩ

እጅግ ብዙ ሰዎች ጉባኤ ነበር

Genesis 50:10

እነርሱም በመጡ ጊዜ

“እነርሱ” የሚለው ቃል በቀብር ሥነሥርዓቱን ይካፈሉ የነበሩ ሰዎችን ያመለክታል

የአጣድ አውድማ

ተገቢ ትርጉሞች 1) “አጣድ” የሚለው ቃል እሾህ ማለት ነው፤ አናም እጅግ ብዙ እሾሆች የሚበቅሉበት መሬት ሊባል ይችላል ወይም 2) “የአውድማው ባለቤት ስም ሊሆን ሊችላል:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ከፍተኛና መራራ ለቅሶ አለቀሱ

እጅግ መራራና ከፍተኛ ልቅሶ አልቅሰው ነበር

ሰባት ቀን

7 ቀን (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

በአጣድ አውድማ

ተገቢ ትርጉሞች 1) አጣድ የተባለው ሰው አውድማ ውስጥ ወይም 2) አጣድ በተባለው አውድማ ውስጥ:: (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ይህ ግብጻዊያን እጅግ ያዘኑበት ጊዜ ነበር

የግብጻዊያን ልቅሶ መራራ ነበር

አቤል ምጽራይም

ተርጓሚዎች የሚከተለውን እንደ ግርጌ ማስታወሻ ሊጠቀሙ ይችላሉ አቤል ምጽራይም የሚለው ስም የግብጻዊያን ሐዘን ማለት ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Genesis 50:12

ልጆቹም

የያዕቆብ ልጆችም

ልክ እንዳዘዛቸው

ልክ መመሪያ እንደሰጣቸው

ልጆቹም ተሸክመውት

ልጆቹም አስከሬኑን ተሸክመውት

ማክፌላ

ማክፌላ የቦታ ወይም የግዛት ስም ነው በዘፍጥረት 23፡9 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

መምሬ

የሔብሮን ከተማ ሌላ ስምዋ ነው በዚያ ይኖር በነበረው በአብርሃም ወዳጅ መምሬ ስም ሳትሰየም አትቀርም፡፡ በዘፍጥረት 13፡ 18 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ኬጢያዊው ኤፍሮን

ይህ የወንድ ሰው ስም ነው ኬጢያዊ የኬጥ ዘር ነው በዘፍጥረት 23፡8 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ወደ ግብጽ ዮሴፍ ተመለሰ

ዮሴፍ ወደ ግብጽ ተመለሰ

አብረውት የነበሩ ሁሉ

አብረውት የሄዱት ሁሉ

Genesis 50:15

ምናልባት ዮሴፍ ቂም ሊበቀለን ይሆናል

እዚህ ቂም ዮሴፍ በእጁ እንደምይዝ ዕቃ ተደርጐ ተገልጾአል አት ምናልባት ዮሴፍ የጠላን ይሆናል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ባደረግንበት ክፋት ሁሉ ብድራት ይመልስብን ይሆናል

እርሱን የበደለውን ሰው መበቀል አንድ ሰው ከሌላ ሰው የተበደረውን እንደመመለስ ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “ባደረግንበት ክፋት ምናልባት ልበቀለን ይችላል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አባትህ ገና ሳይምት እንዲህ ብሎ አዝዞአል ዮሴፍን እንዲህ በሉት እባክህ የወንድምችን በደል ኃጢአታቸውንም ይቅር በል እነርሱ በአንተ ከፍተውብሃልና

ይህ ሁለት ደረጃና ሶስት ደረጃ ጥቅስ ይዞአል እንደተዘዋዋሪ ጥቅስም ሊገለጹ ይችላሉ:: አት “አባትህ ከመሞቱ በፊት እኛ የበደልንህን ይቅር እንዲትለን እንድንነግርህ አዝዞናል” (ጥቅስን በጥቅስ ውስጥ እና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

አባትህ ከመሞቱ በፊት አዝዞናል እንዲህ ስል

ያዕቆብ ለወንድማማቾች ሁሉ አባት ነው:: እዚህ ዮሴፍ አባቱ ለተናገረው ትኩረት እንዲሰጥ “አባትህ” ብለው ይናገራሉ:: አት “አባታችን ከመሞቱ በፊት”

በበደሉህ ጊዜ ያደረጉትን ኃጢአታቸውን

በአንተ ላይ ስላደረጉት ክፉ ነገሮች

አሁንም

ይህ በዚህን ጊዜ ማለት አይደለም ነገር ግን ለሚቀጥለው ዋና ነጥብ ትኩረት እንዲሰጥበት ነው

የአባትህ አምላክ ባሪያዎች የበደሉህን ይቅር በል

ወንድሞቹ ራሳቸውን “የአባትህ አምላክ ባሪያዎች” ብለው ይገልጻሉ:: (አንደኛ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ወገን ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ዮሴፍ ይህን ስሉት አለቀሰ

የሴፍ ይህን መልእክት በሰማ ጊዜ አለቀሰ

Genesis 50:18

በፊቱ ሰግደው

በፊቱ ወደ መሬት ጐንበስ በማለት ሰግደው፤ ይህ የትህትና እና ለዮሴፍ ክብርን የመስጠት ምልክት ነው፡፡ (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

እኔ በእግዚአብሔር ፋንታ ነኝን?

ዮሴፍ ወንድሞቹን ለማደፋፈር ጥያቄ ይጠቀማል:: አት “እኔ በእግዚአብሔር ፋንታ አይደለሁም” ወይም “እኔ እግዚአብሔር አይደለሁም” (አግናኝ ወይም ሽንገላ አዘል ጥያቄዎችን ይመልከቱ)

እናንተ ክፉ ነገር አስባችሁብኝ

እናንተ ክፉ ነገር አድርጋችሁብኝ

እግዚአብሔር ለመልካም አሰበው

እግዚአብሔር ለመልካም አደረገው

ስለዚህ አሁንም አተፍሩ

ስለዚህ እኔን አተፍሩ

እናንተንና ልጆቻችሁን እመግባችኋለሁ

ሁል ጊዜ እናንተና ልጆቻችሁ በቂ ምግብ እንዲኖራችሁ አረጋግጣለሁ

አጽናናቸውም ልባቸውን ደስ አሰኛቸው

እዚህ ልቦች ወንድሞቹን ያመለክታሉ:: አት “አጽናናቸውም ደስም አሰኛቸው” (ክፍልን እንደ ሙሉና ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

Genesis 50:22

መቶ አሥር ዓመት

11ዐ ዓመት (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

የኤፍሬም ልጆች እስከ ሶስት ትውልድ

የኤፍሬም ልጆችና የልጅ ልጆች

ማኪር

ይህ የዮሴፍ ወንድ የልጅ ልጅ ስም ነው (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በዮሴፍ ጭን ላይ ተወለዱ

ይህ አባበል ዮሴፍ እነዚህን የማኪርን ልጆች የራሱ የልጅ ልጆች አድርጐ ተቀበላቸው ማለት ነው:: ይህም ዮሴፍን ለመውረስ ልዩ መብት አላቸው ማለት ነው (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Genesis 50:24

በእርግጥ እናንተን ይጐበኛችኋል

በዘፍጥረት 5ዐ: 24./26 “እናንተ” የሚለው ቃል የዮሴፍን ወንድሞች ነገር ግን ደግሞ የእነርሱን ልጆች ያመለክታል፡: (ምትክ ቃላት አጠቃቀም ይመልከቱ)

ወደ ምድራችሁ ከዚህ ምድር ያወጣችኋል

ከግብጽ ወደ ከነዓን መጓዝ በሚነገርበት ጊዜ “ወደ ላይ መውጣት” የሚለውን ቃለ መጠቀም የተለመደ ነው:: አት “ከዚህ ምድር ያወጣችኋል ወደ ምድራችሁ ይወስዳችኋል” (የክስተቶች ቅደም ተከተል ይመልከቱ)

110 ዓመታት

መቶ አሥር ዓመታት

እነርሱም በመድሃኒት ቀቡት

አንድን አስከሬን ከመቀበሩ በፊት እንዳይፈርስ ለማቆየት መድሃኒት መቀባት ልዩ የሆነ መንገድ ነበር በዘፍጥረት 5ዐ 1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

ኖረ ወይም ተቀመጠ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት “አኖሩት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በአስከሬን ሳጥን ውስጥ

“በሬሳ ሳጥን” ወይም “በሳጥን” ይህ ሳጥን የሞተ ሰው የሚቀመጥበት ነው::


Book: Exodus


Exodus

Chapter 1

1 እያንዳንዳቸው ቤተ ሰባቸውን በመያዝ፣ ከያዕቆብ ጋር ወደ ግብፅ የገቡት የእስራኤል ልጆች ስሞች እነዚህ ናቸው፦ 2 ሮሜል፣ ስምዖን፣ ሌዊ፣ ይሁዳ፣ 3 ይሳኮር፣ ዛብሎን፣ ብንያም፣ 4 ዳን፣ ንፍታሌም፣ ጋድና አሴር። 5 ከያዕቆብ ዘር የተገኙት ሰዎች ሰባ ነበር። ዮሴፍ ቀድሞውኑ በግብፅ ውስጥ ነበረ። 6 ከጊዜ በኋላ ዮሴፍ፣ ወንድሞቹ ሁሉና ያ ትውልድ በሙሉ ሞቱ። 7 ነገር ግን እስራኤላውያን እየተዋለዱ ሄዱ፤ ቊጥራቸውም እጅግ ጨምሮ በጣም ብርቱዎች ሆኑ፤ ምድሪቱንም ሞሏት። 8 በግብፅ ስለ ዮሴፍ የማያውቅ ዐዲስ ንጉሥ ተነሣ። 9 ለሕዝቡም እንደዚህ አለ፤ “እስራኤላውያንን ተመልከቷቸው፤ ከእኛ ይልቅ በቍጥር በዝተዋል፤ እጅግም በርትተዋል። 10 በቍጥር እየበዙ እንዳይሄዱ፣ ጦርነት ቢነሣም ከጠላቶቻችን ጋር ዐብረው እንዳይወጉንና ምድሪቱ ጥለው እንዳይሄዱ ኑ በዘዴ እርምጃ እንውሰድባቸው።” 11 በከባድ ሥራ የሚያስጨንቋቸው አሠሪ አለቆችን በላያቸው ሾሙ። እስራኤላውያን ለፈርዖን ፊቶምና ራምሴ የተባሉ የንብረት ማከማቻ ከተሞችን ሠሩ። 12 ግን ግብፃውያን እስራኤላውያንን ባስጨነቋቸው ቊጥር፣ እስራኤላውያን በቊጥር እየበዙና በምድሪቱ እየተስፋፉ ሄዱ። ስለዚህ ግብፃውያን እስራኤላውያን መፍራት ጀመሩ። 13 ግብፃውያን እስራኤላውያንን በጥብቅ እንዲሠሩ አደረጓቸው። 14 በሸክላ ሥራና ጭቃ በማስቦካት፣ በዕርሻ ውስጥም ሁሉን ዐይነት ከባድ ሥራ በማሠራት አስመረሯቸው (ሕይወታቸውን መራራ አደረጉባቸው) ። የሚጠበቅባቸው ሥራ ሁሉ ከባድ ነበር። 15 ከዚያም በኋላ የግብፅ ንጉሥ ሲፓራና ፉሐ የሚባሉ ዕብራውያት አዋላጆችን እንዲህ አላቸው፤ 16 “ዕብራውያት ሴቶችን በማማጫው ላይ ስታዋልዱ፣ በሚወልዱበት ጊዜ ተመልከቱ። ወንድ ከተወለደ ግደሉት፤ ሴት ከሆነች ግን በሕይወት ትኑር።” 17 ነገር ግን አዋላጆቹ እግዚአብሔርን ፈሩ፣ ንጉሡ ያዘዛቸውንም አልፈጸኩም፤ ትእዛዙን በመፈጸም ፈንታ ሕፃናት ወንዶችን በሕይወት እንዲኖሩ አደረጉ። 18 የግብፅ ንጉሥ አዋላጆቹን ጠርቶ፣ “ለምን ይህን አደረጋችሁ፣ ሕፃናት ወንዶችንስ ለምን አልገደላችኋቸውም?” አላቸው። 19 አዋላጆቹም ለፈርዖን፣ “ዕብራውያት ሴቶች እንደ ግብፃውያት ሴቶች አይደሉም። እነርሱ ብርቱዎች ናቸው፣ የሚወልዱትም አዋላጅ ወደ እነርሱ ከመምጣቱ በፊት ነው” በማለት መለሱለት፥ 20 እግዚአብሔር እነዚህን አዋላጆች ጠበቃቸው። ሕዝቡ በቍጥር በዙ፣ እጅግ ብርቱዎችም ሆኑ። 21 አዋላጆቹ እግዚአብሔርን ስለ ፈሩ፣ እግዚአብሔር ቤተ ሰቦችን ሰጣቸው። 22 ፈርዖን፣ “የተወለደውን ወንድ ልጅ ሁሉ ወንዝ ውስጥ ጣሉ፣ ሴትን ልጅ ግን በሕይወት እንድትኖር ታደርጋላችሁ” በማለት ሕዝቡን ሁሉ አዘዘ።



Exodus 1:1

ቤተሰብ

በአንድ ቤት አብረው የሚኖሩ ሰዎች ስብስብና ከቤተሰብ አባላት ውጭ ሌሎች አገልጋዮችም ጭምር ያሉበት ቤተሰብ ይባላል።

ሰባ ነፍሶች

በቁጥር ሰባ የሚያህሉ ሰዎች ማለት ነው

• ዮሴፍም አስቀድሞ በግብፅ ነበረ

የዮሴፍ ወንድሞች ወደ ግብጽ ከመምጣታቸው በፊት ዮሴፍ በግብጽ ይኖር ነበር

Exodus 1:6

• ወንድሞቹ

ወንድሞቹ የተባሉት የዮሴፍ አስር ታላቅ ወንድሞቹና አንድ ታናሽ ወንድሙ ስብስብ ነው

• ልጆች አፈሩ

ልጆችን አፈሩ የሚለው ሀረግ በተለዋጭ ዘይቤ የተጻፌ ነው። በእስራኤላውያን ዘንድ ልጅ መውልድ ከዛፍ ፍሬ ማፍራት ጋር ተነጻጽሮ ቀርቧል። የዚህ አማራጭ ትርጉም “ብዙ ልጆች ወለዱ” ወይም “ብዙ ልጆችን አገኙ” የሚል ነው።

• ምድሪቱም በእነርሱ ሞላች

ይህ በተደራጊ ግስ የተጻፈ ሲሆን በአድራጊ ግስ “እነርሱ ምድርቱን ሞሉ” ማለት ነው።

• እነርሱ

በሶስተኛ መደብ የተጠራው “እነርሱ” የሚለው ቃል “እስራኤላውያንን” ያመለክታል።

Exodus 1:8

• በግብጽ... ተነሳ

ግብጽ የሚለው ቃል የግብጽ ህዝብን የሚያመለክት ነው። የዚህ አማራጭ ትርጉም “የግብጽ ህዝብን የሚገዛ አዲስ ንጉስ ነገሰ” የሚል ነው።

• እርሱም ህዝቡን

የግብጽ ንጉስ ለህዝቡ እንዲህ ብሎ ተናገረ።

• ህዝቡን

በግብጽ ምድር የሚኖሩ ህዝቦች ወይም ግብጻውያንን ማለት ነው።

• ኑ

ይህ አባባል ንጉሱንና እርሱ የሚመራውን ህዝብ ወይም ግብጻውያንን የሚያጠቃላል ነው። “እኛ” የሚለው መደብ መገለጫ ነው።

• ሰልፍም በተነሳብን ጊዜ

“ሰልፍ” የሚለው ጠላት በእኛ ጦርነት ባወጀ ጊዜ ወይም ጠላት ልወጋን በሚመጣበት ጊዜ የሚለውን ሀሳብ ይገልጻል። “ሰልፍ በተነሳብን” ጊዜ የሚለው በሰውኛ ዘይቤ የተገለጸ ነው፤ ምክንያቱም ሰልፍ እንደ ሰው ተነሳ የሚል አገላለጽ የያዘ ነው።

• ከምድሪቱም እንዳይወጡ

እስራኤላውያን ግብጽን ለቀው እንዳይሄዱ ማለት ነው።

Exodus 1:11

• በብርቱ ሥራም ያስጨንቁአቸው ዘንድ

ግብጻውያን እስራኤላውያንን ከባድ ወይም አስቸጋሪ ሥራ እንዲሰሩ ያስጨንቋቸው ነበር ማለት ነው።

• ግብር አስገባሪዎች

እስራኤላውያን ከባድ ሥራ እንዲሰሩ የሚያስገድዱ የግብጽ “አሰሪ አለቆች” ማለት ነው።

• ጽኑ ከተሞች ... ሠሩ

ንጉሱና ሌሎች መሪዎች ወይም ሹማምንት ምግብና ሌሎች ተፈላጊ የሆኑ ንብረቶችን የሚያኖሩበት “ንብረት ማከማቻ ከተሞች” ማለት ነው።

Exodus 1:13

• በመከራ ገዙአቸው

ጭካኔ በተሞላበትና ርህራሄ በለሌው ስሜት ግፍ ይፈጽሙባቸው ነበር።

• ሕይወታቸውን ያስመርሩአቸው ነበር

የአንድ ዛፍ ፍሬ መራራ ከሆነ እንደማይበላና ደስ እንደማይል ሁሉ የእስራኤላውያን ህይወት እለት ተዕለት በሚደርስባቸው ጭካነ መራራ በመሆኑ ደስተኞች አልነበሩም ማለት ነው። አባባሉ በተለዋጭ ዘይቤ የተገለጸ ነው።

• በጡብ ሥራ

ለቤት ሥራ የሚውል ከጭቃና ከሸክላ አፈር እንዲሁም በዘመናዊ መንገድ ከሲሚንቶ የሚሰራ ብሎኬት መሳይ ነገር ማለት ነው

• በመከራም በሚያሠሩአቸው ሥራ ሁሉ

ግብጻውያን እስራኤላውያንን የተለያዩና በጣም ከባድ የሆነ የጉልበት ሥራዎችን ያሰሩአቸው ነበር።

Exodus 1:15

• የግብፅም ንጉሥ

የግብጽ ንጉስ በወል ወይም በጋራ ስም “ፈርዖን” ተብሎ ይጠራል።

• አዋላጆች

ሴቶች በሚወልዱበት ጊዜ የማዋለድ ሥራ የሚሰሩ ወይም አገልግሎት የሚሰጡ ሴቶች ማለት ነው

• ሲፓራና ፉሐ

የዕብራውያን ሴቶች ስም ነው (ስሞችን የመተርጎም ዘዴ ተመልከት)

• የማማጫ ድንጋይ (መቀመጫ)

ሴቶች በሚወልዱበት ጊዜ የሚቀመጥቡት ድንጋይ ወይም መቀመጫ ማለት ነው። እስራኤላውያን ሴቶች ለመውለድ በዚህ ድንጋይ ላይ ሲቀመጡ ወይም ሴቶቹ በሚወልዱበት ጊዜ ማለት ነው።

Exodus 1:18

• ለምን እንዲህ አደረጋችሁ? ወንዶቹን ሕፃናትንስ ለምን አዳናችሁ?፦

ፈርዖን ይህንን ጥያቄ አዋላጆችን የጠየቀው ወንድ ህጻናትን ባለመግደላቸው ምክንያት ልገስጻቸው ፈልጎ ነው። ይህ ጥያቄ በመደበኛ ዓረፍተ ነገር ሲተረጎም “ወንድ ህጽናትን ባለመግደላችሁ ትዕዛዜን ተላልፋችሁኋል” የሚል ይሆናል። ጥያቄው በባህርዩ አጋናኝ ጥያቄ ነው።

• የዕብራውያን ሴቶች እንደ ግብፃውያን ሴቶች አይደሉም

አዋላጆች የንጉሱን ቁጣ ለማብረድ በጥበብና በምክንያታዊነት የተናገሩት ንግግር ዓይነት ነው።

Exodus 1:20

• ለአዋላጆቹ መልካም ሆነላቸው

ፈሪዖን እነዚህን ሴቶች እንዳይገድላቸው እግዚአብሔር ጠበቃቸው፥ ተከላከላቸው፥ ለክፉ አሳልፎ አልሰጣቸውም ማለት ነው።

• እግዚአብሔርን ስለ ፈሩ

እግዚአብሔር ከሁሉ በላይ ገዥ እንደሆነ አምነው ከፈሪዖን ይልቅ እግብቻ ሰሙ ማለት ነውዚአብሄርን ፈሩ፥ ለእርሱ ብቻ ታዘዙ፥ እርሱን

• ለያንዳንዳቸውም ቤተሰብ ሰጣቸው

እግዚአብሔር ለእነዚህ አዋላጆች ቤተሰብ ወይም ልጅ ወይም ዘር ሰጣቸው ማለት ነው።

• የሚወለደውን ወንድ ልጅ ሁሉ እያነሣችሁ ዓባይ ወንዝ ውስጥ ጣሉ

ወንዶች ልጆች ውሃው ውስጥ ሰጥመው እንድሞቱ ህዝቡ እያንዳንዱን ወንድ ልጅ ወደ አባይ ወንዝ እንድጥል ጥብቅ ትዕዛዝ ንጉሱ ሰጣቸው።


Chapter 2

1 ከሌዊ ወገን የሆነ አንድ ሰው ሌዋዊት ሴት አገባ፡፡ 2 ሴትዮዋ ፀነሰች ወንድ ልጅም ወለደች፡፡ ሕፃኑ መልከ መልካም መሆኑን ስታይ፣ ሦስት ወር ሸሸገችው፡፡ 3 ከዚያ በላይ ልትሸሽገው ባልቻለች ጊዜ፣ የደንገል ቅርጫት ወስዳ በዝፍትና በቅጥራን ለቀለቀችው፡፡ ከዚያም ልጁን በውስጡ አስተኝታ ውሃው ውስጥ በቄጠማው መካከል በወንዙ ዳርቻ አስቀመጠችው፡፡ 4 የሚያጋጥመውን ለማየት የሕፃኑ እኅት በርቀት ቆማ ነበር፡፡ 5 ጠባቂዎቿ በወንዙ ዳር እየሄዱ ሳለ፣ የፈርዖን ልጅ በወንዙ ለመታጠብ ወረደች፡፡ ልዕቲቱ ቅርጫቱን በቄጠማዎች መካከል አየችው፡፡ ቅርጫቱን እንዲያመጣላት ጠባቂዋን ላከች፡፡ 6 ቅርጫቱን ስትከፍተው፣ ሕፃኑን አየች፡፡ እነሆ፣ ሕፃኑ ያለቅስ ነበር፡፡ ራራችለትና፣ «ይህ በእርግጥ ከዕብራውያን ልጆች አንዱ ነው» አለች፡፡ 7 ከዚያም በኋላ የሕፃኑን እኅት የፈርዖንን ልጅ፣ «ልሂድና ሕፃኑን የምታሳድግልሽ ዕብራዊት ሴት ልፈልግልሽ?» አለቻት፡፡ 8 የፈርዖንም ልጅ «ሂጂ» አለቻት፡፡ ወጣቷም ልጅ ሄዳ የሕፃኑን እናት አመጣች፡፡ 9 የፈርዖን ልጅ የሕፃኑን እናት፣ «ይህ ሕፃን ውሰጅና አሳድጊልኝ፤ ደሞዝ እከፍልሻለሁ» አለቻት፡፡ ሴትዮዋም ሕፃኑን ወስዳ አሳደገችው፡፡ 10 ሕፃኑ ባደገ ጊዜም ወደ ፈርዖን ልጅ አመጣችው፤ የልዕልቲቱም ልጅ ሆነ፡፡ «ከውሃ አውጥቼዋለሁና» ብላም ስሙን ሙሴ አለችው፡፡ 11 ሙሴ ባደገ ጊዜ ወደ ወገኖቹ ሄዶ የሚሠሩትን ከባድ ሥራ ተመለከተ፡፡ ከገዛ ወገኖቹ መካከል አንዱን ዕብራዊ አንድ ግብፃዊ ሲደበድበው አየ፡፡ 12 ግራና ቀኙን ተመልክቶ ማንም አለመኖሩን ሲያረጋግጥ፣ ግብፃዊውን ገድሎ በአሸዋ ውስጥ ደበቀው፡፡ 13 ቀን ሙሴ ወደ ውጭ ወጣ፤ እነሆም ሁለት ዕብራውያን ወንዶች እየተጣሉ ነበር፡፡በደለኛ የነበረውን ሰውየ፣ «ባልንጀራህ ለምን ትደበድበዋለህ?» አለው፡፡ 14 ሰውየው ግን፣ «አንተን በእኛ ላይ አለቃና ዳኛ ማን አደረገህ? ያን ግብፃዊ እንድ ገደልኸው እኔንም ልትገድለኝ ታስባለህ?» አለ፡፡ ሙሴም ፈራና፣ «ያደረግሁት በሌሎች ሰዎች ዘንድ በእርግጥ ታውቋል» አለ፡፡ 15 ስለ ጉዳዩ ሲሰማ ሙሴን ሊገድለው ፈለገ፡፡ ነገር ግን ከፈርዖን ሸሽቶ በምድያም አገር ኖረ፡፡ እዚያም በአንድ የውሀ ጉድጓድ አጠገብ ተቀመጠ፡፡ 16 ካህን ሰባት ሴት ልጆች ነበሩት፡፡ እነርሱም ወደ ጉድጓዱ መጥተው ውሀ ቀዱ፣ የአባታቸውን መንጋ ለማጠጣትም ገንዳውን ሞሉት፡፡ 17 መጥተው ሊያባርሯቸው ሞከሩ፣ ነገር ግን ሙሴ ሄዶ ዐገዛቸው፡፡ መንጋቸውንም አጠጣላቸው፤ 18 ወደ አባታቸው ወደ ራጉኤል ሲሄዱም፣ አባታቸው፣ «ዛሬ እንዴት ቶሎ ወደ ቤት መጣችሁ?» አለ፡፡ 19 «አንድ ግብፃዊ ከእረኞች አዳነን፤ ውሀም ቀድቶ መንጋውን አጠጣልን» አሉ፡፡ 20 ልጆቹን፣ «ታዲያ የት አለ?» ሰውየውን ለምን ተዋችሁት? ምግብ ከእኛ ጋር እንዲበላ ጥሩት» አላቸው፡፡ 21 ሲፓራን እንዲያገባትም እንኳ ከሰጠው ሰውየ ጋር ለመኖር ሙሴ ተስማማ፡፡ 22 ወንድ ልጅ ወለደች፤ ሙሴም፣ «የባዕድ ምድር ኗሪ ነኝ» ሲልም ስሙን ጌርሳም አለው፡፡ 23 ከረጅም ጊዜ በኋላ፣ የግብፅ ንጉሥ ሞተ፡፡ እስራኤላውያን ከባርነት ሥራ የተነሣ አለቀሱ፣ ለርዳትም ጮኹ፤ ከባርነት ቀበራቸው የተነሣም ያሰሙት ጩኸት ወደ እግዚአብሔር ወጣ፡፡ 24 እግዚአብሔር ልቅሶአቸውን ሲሰማ ከአብርሃም፣ ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጋር የገባውን ቃል ኪዳኑን ዐሰበ፡፡ 25 እግዚአብሔር እስራኤላውያንን አየ፤ ሁኔታቸውንም ተረዳ፡፡



Exodus 2:1

• በዚያን ጊዜ

በዕብራይስጡና በቀድሞ አማርኛ ትርጉም (በ1954 ትርጉም) ይህ አገናኝ ሀረግ የለም። ነገር ግን በአንዳንድ እንግሊዘኛና በሌሎች አማርኛ ትርጉሞች እንደ አገናኝ ሀረግ የገባ ነው። ይህ አገናኝ ሀረግ አዲስ ሀሳብ ሲጀመር ወይም አንድ ታሪክ አልቆ ሌላ ታሪክ ሲጀመር የሚያሳይ ነው። ንጉሱ የዕብራውያን ወንድ ልጆች እንዲገደሉ ባዘዘበት ጊዜ ሌላ ታሪክ ሲከሰት ያሳየናል። ተርጓሚዎች በቋንቋቸው እንደዚህ ያሉ እገናኝ ሀረጎች ወይም ቃላት መኖሩን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል።

Exodus 2:3

• የደንገል ሣጥን

በናይል ወንዝ ዳር የሚበቅልና የሚያድግ ከቀጤማ፥ ከመቃ፥ ወይም ከሸምበቆ የተሰራ ቅርጫት መሳይ ነገር ነው።

• ዝፍትና ቅጥራን

ለአስፋልት መንገድ ሥራ የሚጠቅም ቃጥራሜ ወይም ሬንጅ ዓይነት ነገር ነው። ውሃ ወደ ቅርጫቱ እንዳይገባ ወይም እንዳይሰርግ የሚያደርግ ነገር ነው። ጥቁር ወይም ቡናማ ቀለም ያለው ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት እና ከዛፍ ላይ የሚገኝ ሲሆን በተፈጥሮ የማጣበቅ ባህርይ ያለው ነው።

• ለቀለቀችው

ውሃ ወደ ውስጥ እንዳይገባ ለጠፈችው ወይም አሸገችው ማለት ነው።

• ቄጠማ

በወንዝ ዳር ወይም ደግሞ እርጥበት ባለበት አከባቢ የሚበቅል ረጅም ሳር መሳይ ነገር ነው፥ ምናልባት ሸምበቆ በሌለበት ወይም በማይታወቅበት ማህበረሰብ ውስጥ ሸምበቆ ወይም ቀርከሃ በምትክነት መጠቀም ይቻላል።

• ራቅ ብላ ቆማ ታይ ነበር

ሌሎች አይተዋት ማን እንደሆነች እንዳይጠቋትና እንዲሁም ህጻኑን ማየትና መከታተል በምትችልበት ርቀት ላይ ቆማ ሁኔታውን እየተከታተለች ነበር ማለት ነው።

Exodus 2:5

• ደንገጥሮችዋም

አገልጋዮቹዋ እንደ ማለት ነው። በተለይ በንጉሱ ሴት ልጅ ላይ ምንም ጉዳት እንዳይደርስባትና ብቸኛ እንዳትሆን የሚጠብቋት አገልጋዮቿ ናቸው።

• በዚህ ጊዜ

በታሪኩ መካከል ላይ ሌላ ጣልቃ ገብ ታሪክ ሲከሰት “በዚህን ጊዜ” በማለት የአንባቢን ትኩረት ይስባል። ይህ አገናኝ ሀረግ በቀድሞና በአዲሱ አማርኛ ትርጉም ላይ እንዲሁም በዕብራይስጡ ላይ አልተጠቀሰም።

Exodus 2:7

• ታጠባልሽ ዘንድ

ሕፃኑን እያጠባች የምታሳድግ ሴት ማለት ነው።

Exodus 2:9

• ሕፃን ወስደሽ አጥቢልኝ

ይህን ሕፃን ወስደሽ እያጠባሽ አሳድጊልኝ

• ለእርስዋም ልጅ ሆነላት

ልጁም የፈርዖን ሴት ልጅ የማደጎ ልጅ ሆነላት ማለት ነው

• ከውኃ አውጥቼዋለሁና

ሙሴ የሚለው የስሙ ትርጉም በዕብራይስጥ ቋንቋ “ማውጣት” የሚል ፍቺ ስላለው ተርጓሚዎች የግርጌ ማስታወሻ በመስጠት የስሙን ፍቺ ግልጽ ሊያደርጉ ይችላሉ።

Exodus 2:11

• የዕብራውያንን ሰው ሲመታ አየ

አንድ ግብፃዊ ሰው ዕብራዊ ወገኑን ሲደበድበው ማየቱን የሚገልጽ ነው

• ወዲህና ወዲያም ተመለከተ

ይህ ሁለት ተቃራኒ አቅጣጫዎች ጠቋሚ አገላለጽ አካባቢውን ቃኝቶ ሰው አለመኖሩን ለማጣራት ሁሉንም አቅጣጫ ተመለከተ የሚል አጠቃላይ ፍቺ ይዟል

Exodus 2:13

• በሁለተኛውም ቀን ወጣ

ሙሴ በማግስቱ እየሆነ ያለውን ነገር ለማየትና ለማጣራት መውጣቱን ለመግለጽ ነው

• በዳዩንም

ጥላቻውን የጀመረውን ወይም ጥፋተኛውን ወይም ጓደኛውን ቀድሞ መምታት የጀመረውን ዕብራዊ ወገኑን ማለት ነው። ይህ አባባል በዕብራውያን ዘንድ የታወቀና በባህሉ የተለመደ አባባል ነው።

• በእኛ ላይ አንተን አለቃ ወይስ ዳኛ ማን አደረገህ?

ይህ ጥያቄ የሚያሳየው ሙሴ በሁለቱ ሰዎች መካከል ጣልቃ በመግባቱ ነገሩን ሳታጣራ ወይም በትክክል ሳትረዳ ለምን አለቃ ትሆናለህ ብሎ ለመገሰጽ የተጠቀመበት አባባል ነው። ይህ አጋናኝ ጥያቄ በመደበኛ ዐረፍተ ነገር ሲተረጎም “አንተ በእኛ ላይ ለመፍረድና መሪ ለመሆን አልተጠራህም” እንደ ማለት ነው።

• ግብፃዊውን እንደገደልኸው ልትገድለኝ ትሻለህን?

ይህ አጋናኝ ጥያቄ የሚያመለክተው ውስጠ ወይራ ወይም አሽሙር ነው። አማራጭ ትርጉሙ፦ ትናንትና አንድ ግብጻዊ እንደገደልክ እናውቃለን፥ እኔን ግን አትገድለኝም” ሊሆን ይችላል።

Exodus 2:15

• ፈርዖንም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ

በታሪኩ ውስጥ ፀሐፊው ሌላ ሀሳብ ሲያስገባ ወይም አዲስ የታሪክ ክፍል ሲጨምር እንመለከታለን። ሙሴ ያደርገውን ነገር ፈርዖን ሰምቶታል ማለት ነው ወይም ወሬው ወደ ፈርዖን ደረሰ ማለት ነው።

• ለምድያምም ካህን ሰባት ሴቶች ልጆች ነበሩት

ጸሐፊው በታሪኩ ውስጥ አዳዲስ ሰዎችን ወይም ተዋንያንን ሲጨምር እናያለን፥

• እነርሱም መጥተው ውኃ ቀዱ

በጊዜው ዕብራውያን ውሃ የሚቀዱት ከጉድጓድ ነበርና ውሃ ለመቅዳት ወደ ጉድጓዱ እንደመጡ ያሳያል።

• ገንዳ

ከእንጨት ወይም ከድንጋይ ወይም ከሌሎች ነገሮች የሚሰራ ከብቶችን ውሃ ለማጠጣት ወይም መኖ ለመስጠት የሚያገለግል ነው።

• እረኞችም መጥተው ገፉአቸው

እረኞችም መጥተው እነዚያን ሴቶች አባረሩአቸው፥ ከለከሉአቸው፥ አሳደዱአቸው እንደማለት ነው።

• ሙሴ ግን ተነሥቶ ረዳቸው

እረኞችም መጥተው ሴቶቹን ሲያባርሯቸው ሙሴ ከተቀመጠበት ተነሥቶ ተከላከለላቸው፥ ከእረኞችም እጅ አዳናቸው ወይም አስጣላቸው ማለት ነው።

Exodus 2:18

• ለምንስ ያንን ሰው ተዋችሁት?

ይህ ጥይቄ አነስተኛ የሆነ ቁጣ አዘል ንግግር ወይም ጥያቄ ነው። እንደ ዕብራውያን ባህል እነዚህ ሴቶች ልጆች ይህን ሰው በእንግድነት ወደ ቤታቸው መጋበዝ ነበረባቸው። በቀጥታ ዐረፍተ ነገር ሲነገር “ይህን ሰው በጉድጓድ ውሃው አጠገብ ትታችሁ መምጣት አልነበረባችሁም”

Exodus 2:21

• ሙሴም ከዚያ ሰው ጋር ሊቀመጥ ወደደ

ሙሴም ከሰውየው ወይም ከራጉኤል ጋር ለመኖር ተስማማ ወይም ፈቃደኛ ሆነ ማለት ነው።

• ጺጳራን

የራጉኤል ሴት ልጁ ነች

• ጌርሳም

የሙሴ ታላቅ ልጁ ነው

• በሌላ ምድር መጻተኛ ነኝ

በሰው አገር መጤ ወይም እንግዳ ነኝ ማለት ነው

Exodus 2:23

• አለቀሱ

ከመከራቸውና ከጭንቃቸው የተነሳ ማልቀሳቸውን የሚያሳይ ነው

• ጩኸታቸው ወደ እግዚአብሔር ወጣ

የእስራኤላውያን ጩኸት እግር እንዳለው ሰው ወደ እግዚአብሔር እንደተጓዘ ወይም እንደሄደ በሰውኛ ዘይቤ የተነገረ ነው። በቀጥተኛ ዐረፍተ ነገር ሲነገር “እግዚአብሔር ጩኸታቸውን ሰማ” የሚል ነው።

• እግዚአብሔር . . . ቃል ኪዳኑን አሰበ

ይህ አባባል በዕብራውያን ዘንድ የተለመደ ነው። ሰው አንድን ነገር ረስቶ እንደገና እንደሚያስብ የተነገረ ዘይቤያዊ ንግግር ነው። በሌላ አገላለጽ፦ “እግዚአብሔር የገባውን ቃል ኪዳን አሰበ”።


Chapter 3

1 ሙሴ የምድያምን ካህን፣ የዐማቱን የየቶርን በጎች ጠብቅ ነበር፡፡ በጎቹን ወደ ምድረ በዳው ዳርቻ ነድቶ ወደ እግዚአብሔር ተራራ ወደ ኮሬብ ደረሰ፡፡ 2 በዚያም የእግዚአብሔር መልአክ በቊጥቋጦ ውስጥ በእሳት ነበልባል ተገለጠለት፡፡ ሙሴ ተመለከተ፣ እነሆም ቊጥቋጦው እየተቀጣጠለ ነበር፤ ነገር ግን ቊጥቋጦው አልተቃጠለም፡፡ 3 ሙሴም፣ «ልቅረብና ቊጥቋጦው ለምን እንዳልተቃጠለ ይህን አስደናቂ ነገር ልይ» አለ፡፡ 4 ሊመለከት እንደ ቀረበ እግዚአብሔር ሲያየው፣ ከቊጥቋጦው ውስጥ ጠራው፤ «ሙሴ፣ ሙሴ» አለውመ፡፡ ሙሴም፣ «እነሆኝ» አለ፡፡ 5 እግዚአብሔር፣ «አትቅረብ! የቆምህበት ምድር ለእኔ ተቀድሶአልና ጫማህን አውልቅ» አለው፡፡ 6 ደግሞም፣ «እኔ የአባትህ አምላክ፣ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክ፣ የያዕቆብ አምላክ ነኝ» አለው፡፡ ከዚያም በኋላ ሙሴ እግዚአብሔርን ማየት ስለ ፈራ ፊቱን ሸፈነ፡፡ 7 እንዲህ አለ፤ «በግብፅ የሚኖሩትን የሕዝቤን ሥቃይ በእርግጥ አይቻለሁ፡፡ አሠሪ አለቆቻቸው ከሚያደርሱባቸው ጭቈና የተነሣ ጩኸታቸውን ሰምቻለሁ፤ ስለ ሥቃያቸው ዐውቃለሁና፡፡ 8 ከግብፃውያን አገዛዝ ነጻ ላወጣቸውና ከዚያም ጋር አውጥቼ ማርና ወተት ወደምታፈሰው መልካምና ለም ወደሆነችው፤ ወደ ከነዓናውያን፣ ኬጢያውያን፣ አሞራውያንን፣ ፌርዛውያን፣ ኤውያውያንና ኢያቡሳውያን ምድር ላሰገባቸው ወርጃለሁ አለ፡፡ 9 የእስራል ሕዝብ ጩኸት ወደ እኔ ደርሶአል፡፡ ይልቁንም ግብፃውያን ያደረሱባቸውን ጭቈና አይቻለሁ፡፡ 10 ስለዚህ ሕዝቤን፣ እስራኤላውያንን ከግብፅ እንድታወጣ ወደ ፈርዖን እልክልሃለሁ፡፡» 11 ግን፣ እግዚአብሔርን «ወደ ፈርዖን የምሄድና እስራኤላውያንን ከግብፅ የማወጣቸው እኔ ማን ነኝ?» አለው፡፡ 12 ሙሴን መልሶ፣ «እኔ ከአንተ ጋር እሆናለሁ፡፡ ይህ እኔ እንደ ላክሁህ ምልክት ይሆናል፡፡ ሕዝቡን ከግብፅ ስታወጣቸው፣ በዚህ ተራራ ላይ ታመልኩኛላችሁ» አለው፡፡ 13 ሙሴም እግዚአብሔርን፣ «ወደ እስራኤላውያን ስሄድና ‹የአባቶቻችሁ አምላክ ወደ እናንተ ልኮኛል› ብዬ ስነግራቸው፣ እነርሱም፣ «ስሙ ማን ነው? ሲሉኝ ምን እነግራቸዋሉ? አለው፡፡ 14 እግዚአብሔርም ሙሴን፣ «እኔ ያለሁ የምኖርም ነኝ፡፡ ያለና የሚኖር ወደ እናንተ ልኮኛል ብለህ ለእስራኤላውያን ንገራቸው» አለው፡፡ 15 ደግሞም እግዚአብሔር ለሙሴ እንዲህ አለ፤ እግዚአብሔር የአባቶቻችሁ አምላክ፣ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክ፣ የያዕቆብ አምላክ ወደ እናንተ ልኮኛል፡፡ ስሜ ለዘለዓለም ይህ ነው፤ ለትውልዶች ሁሉ የታስበውም በዚህ ነው ብለህ ለእስራኤላውያን ንገራቸው፡፡» 16 ሂድና የእስራኤልን ሽማግሌዎች ሰብስብ፤ እንዲህም ብለህ ንገራቸው፤ የአባቶቻችሁ አምላክ፣ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክ፣ የያዕቆብ አምላክ እግዚአብሔር ለእኔ ተገለጠልኝ፤ እንዲህም አለኝ፣ «ጐብኝቻችኋለሁ፤ በግብፅ ውስጥ የደረሰባችሁንም አይቻለሁ፡፡ 17 በግብፅ ከደረሰባችሁ ጭቈና ነጻ ላወጣችሁና ማርና ወተት ወደምታፈሰው ወደ ከነዓናውያን፣ ወደ ኬጢያውያን፣ ወደ አሞራውያን፣ ወደ ፌርዛውያን፣ ወደኤዊያውያንና ወደ ኢያቡሳውያን ምድር ላገባችሁ ቃል ገብቻለሁ፡፡» 18 ሽማግሌዎቹም ይሰሙሃል፡፡ አንተና የእስራኤል ሽማግሌዎች ወደ ግብፅ ንጉሥ ሂዱና፣ የዕብራውያን አምላክ እግዚአብሔር ተገለጠልን፡፡ ስለዚህም ለአምላካችን ለእግዚአብሔር መሠዋት እንድንችል በምድረ በዳው ውስጥ የሦስት ቀን ጕዞ እንሂድ በሉት፡፡ 19 ነገር ግን የግብፅ ንጉሥ እጁ ካልተገደደ በቀር ለመሄድ እንደማይፈቅድላችሁ ዐውቃለሁ፡፡ 20 በመካከላቸው በማድረጋቸው ተአምራት ሁሉ ግብፃውያንን እመታቸዋለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ፣ እንድትሄዱ ይፈቅድላችኋል፡፡ 21 ሕዝብ ከግብፃውያን ዘንድ መወደድን እንዲያገኝ አደርጋለሁ፣ ስለዚህ ስትወጡ፣ ባዶ እጃችሁን አትወጡም፡፡ 22 ሴት ከግብፃውያት ጎረቤቶቿና በጎረቤቶቿ ቤቶች ውስጥ ከምትኖር ማንኛውም ሴት የብርና የወርቅ ጌጣጌጦች፣ ልብስም እንዲሰጣት ትጠይቃለች፡፡ እነርሱንም በወንዶችና በሴቶች ልጆቻችሁ ላይ ታደርጓቸዋላችሁ፡፡ ግብፃውያንን በዚህ መንገድ ትበዘብዟቸዋላችሁ፡፡



Exodus 3:1

• የእግዚአብሔር መልአክ

አንድ የተለየ የእግዚአብሔር መልዓክ ወይም መልዕክተኛ ማለት ነው።

• እግዚአብሔር

በዕብራይስጡ ያህዌ ተብሎ የሚጠራው ስም ነው። አንዳንድ የእንግሊዘኛ ትርጉሞች ይህን “YHWH” የሚለውን ስም “LORD” ይላሉ፤ ይህ ስም አዶናይ “ጌታ” ከሚለው ስም ይለያል። የእንግሊዘኛ ትርጉሞች ይህንን ስም ለመለየት “Lord” ብለዋል። በአማርኛችን “ያህዌ” እና “ኤሎሂም” የሚለው ስም “እግዚአብሔር” በሚለው ስም ተጠቅሶ እናገኛለን።

• እነሆም

ይህ ገላጭ ቃል ለሰው ወይም ለግዑዝ ነገር ሊውል ይችላል። በዕብራይስጡ አዲስ ሀሳብ ለመግለጽ ወይም አዲስ ሀሳብ መኖሩን ለማሳየት ወይም ዕውቅና ለመስጠት የሚጠቀሙበት ነው።

Exodus 3:4

• ጫማህን ከእግርህ አውጣ

“ራስህን ቀድስ” ወይም “ራስህን ለእግዚአብሔር ለይ” የሚል ነው

• እኔ የአባትህ አምላክ

ይህ አባባል ሁለት ትርጉሞች ይኖሩታል፦ 1) የአባትህ 2) ቅድሜ አያትህ የሚል ሊሆን ይችላል። በዚህ ክፍል ትርጉሙ “ቅድሜ አያትህ” የሚል ከሆነ የአብርሃም፥ የይስሃቅ እና የያዕቆብ አምላክ የሚለው ትክክለኛ ትርጉም መሆኑ ነው። “አባትህ” የሚለው ከሆነ “የሙሴ አባት” መሆኑ ነው።

Exodus 3:7

• ከአስገባሪዎቻቸውም የተነሣ

እስራኤላውያን ከባድ ሥራ እንዲሰሩ የሚያስገድዱ የግብጽ “አሰሪ አለቆች” ወይም “አሠሪዎቻቸው” ማለት ነው። ከምዕራፍ 1፡11 ጋር ተመሳሳይነት አለው።

• ወተትና ማር ወደምታፈስሰው

ይህ ሐረግ በግነታዊ እና በተለዋጭ ዘይቤ የተገለጸ ነው። ይህ አገላለጽ ከምድሪቱ ወተትና ማር ይፈልቃል ማለት ሳይሆን ለከብት ርባታና ለእርሻ በጣም ምቹ የሆነ ምድር እንደሆነ ለማሳየት ነው። እንዲሁም “የምታፈስ” አገር የሚለው ቃልም ሁሉም ነገር የሞላባት ምድር የሚል ፍቺ ያለው ነው።

• ወተት

በእንስሳት ምርትና ተዋጽኦ የዳበረች አገር መሆኑዋን ለማመልከት ነው

• ማር

በእስራኤል ምድር ማር በሁለት መንገዶች ይመረታል። አንደኛው ከከብት እርባታ የሚገኘው ሲሆን ሁለተኛው ከተምር ዛፍና ከሌሎች ዕጽዋት የሚገኘው ነው።

Exodus 3:9

• የሕዝቤ የእስራኤል ጩኸት ወደ እኔ ደርሶአል

እዚህ ጋር ጩኸታቸው ወደ እኔ ደርሷል ሲል ጩኸት እጅና እግር አውጥቶ እንደተራመደ አድርጎ ያቀርባል። ይህ በሰውኛ ዘይቤ የቀረበ ሲሆን “እግዚአብሔር የእስራኤል ሰዎች ጩኸት ሰምቷል” የሚል ነው።

Exodus 3:11

• ወደ ፈርዖን የምሄድ የእስራኤልንም ልጆች ከግብፅ የማወጣ እኔ ማን ነኝ?

ሙሴ ይህን ጥያቄ እግዚአብሔርን ሲጠይቅ እርሱ ደካማ ሰው መሆኑንና ማንም ሰው እርሱ የሚለውን አይሰማም ብሎ በማሰቡ ነበር። በመደበኛ ንግግር “እኔ ወደ ፈርዖን ለመሄድና የእስራኤልን ልጆች ከግብጽ ለማውጣት በቁ ሰው አይደለሁም” ማለቱ ነው።

Exodus 3:13

• ያለና የሚኖር እኔ ነኝ

ስሙ ማን እንደሆነ ሙሴ ለጠየቀው ጥያቄ እግዚአብሔር ሲመልስ እኔ “ያለሁና የምኖር ነኝ” ስለሆንኩ ስሙ “ ‘እኔ ነኝ’ የሆነ እግዚአብሔር ወደ እናንተ ልኮኛል” ብለህ ንገራቸው አለው።

• ያለና የሚኖር

የዚህ ሀረግ አገላለጽ በሁለት መንገድ ልተረጎም ይችላል። 1) “ያለና የሚኖር ነኝ” የሚለው ሀረግ ስሙ ሊሆን ይችላል፤ 2) እግዚአብሔር ስሙን ሳይሆን ማንነቱን ለሙሴ እየነገረው ሊሆን ይችላል። ስለሆነም እግዚአብሔር ዘላለማዊ ስለሆነ ትናንት የነበረ፥ ዛሬም ያለና ነገም የሚኖር አምላክ ነው።

• እኔ ነኝ

ይህ ስም ለትርጉም አስቸጋሪ ሊሆን ስለሚችል “እኔ ሕያው ነኝ” በሚል ልተረጎም ይችላል።

Exodus 3:16

አጠቃላይ ዕይታ፦ እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል • የአባቶቻችሁ አምላክ የአብርሃም የይስሐቅም የያዕቆብም አምላክ

እነዚህ ሶስቱ ሰዎች የሙሴ ቅድሜ አያቶች ናቸው፥ እንዲሁም የእስራኤላውያንም ቅድሜ አያቶች ናቸው።

• መጎብኘትን ጎበኘኋችሁ

እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ቀድሞ እንዳያቸውና እንደተመለከታቸው እንዲሁም እንደጎበኝቸው ይሳያል።

• እነርሱም ቃልህን ይሰማሉ

“እነርሱ” የተባለው የእስራኤል ሽማግሌዎች ሲሆኑ “ቃልህን” የተባለው ደግሞ ሙሴ የሚናገረውን ቃል እንደሚሰሙ ለማመልከት ነው።

Exodus 3:19

አጠቃላይ ዕይታ፦ እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል • በጽኑ እጅ ካልሆነ በቀር

“በጽኑ እጅ” ምትካዊ ዘይቤ ሲሆን የሀይል ምንጭ የሆነውንና የእጁን ባለቤት አመልካች ነው። የዚህ ሀረግ ሁለቱ ፍቺዎች፦ 1) ፈርዖን ምንም ለማድረግ አቅም እንደለሌው 2) ፈርዖን እንዲለቅ እግዚአብሔር ሲፈቅድ ብቻ መሆኑን ለማመልከት ነው።

• እኔም እጄን እዘረጋለሁ

እግዚአብሔር በታላቅ ሀይሉ ሲያጠቃው ወይም ሲያስገድደው እንደ ማለት ነው። እኔ እጄን እዘረጋለሁ ሲል “ሀይሌን እገልጣለሁ” ማለቱ ነው።

• ባዶ እጃችሁን አትሄዱም

የዚህ ሀረግ ተቃራኒ ሀሳቡ ብዙ ነገሮችን ይዛችሁ፤ ውድና ያጌጡ ነገሮችን አግኝታችሁ በሙላት ትሄዳላችሁ ማለት ነው። የአገላለጹ ምክንያት ትኩረት ለመስጠት ነው።

• ከጎረቤትዋ በቤትዋም ካለችው ሴት

ይህ አባባል 1) በእስራኤላዊት ጎረበት ከምትገኘው ከግብጻዊት ሴት፤ 2) በእስራኤላዊት ጎረበት የምትገኘው ቤት ከምትኖር ሴት ማለት ሊሆን ይችላል።


Chapter 4

1 ሙሴም መልሶ፣ «ባያምኑኝስ ወይም ባይሰሙኝ ነገር ግን በምትኩ፣ እግዚአብሔር አልተገለጠልህም» ቢሉኝስ? 2 እግዚአብሔር ሙሴን፣ «በእጅህ ያለው ምንድን ነው?» አለው፡፡ ሙሴም «በትር» አለ፡፡ 3 እግዚአብሔር፣ «መሬት ላይ ጣለው» አለው፡፡ ሙሴም በትሩን መሬት ላይ ጣለው፤ በትሩም እባብ ሆነ፡፡ ሙሴ ከእባቡ ሸሸ፡፡ 4 እግዚአብሔር ሙሴን፣ «እጅህን ዘርግተህ የእባቡን ጅራት ያዝ» አለው፡፡ ሙሴም እጁን ዘረገና እባቡን ያዘው፡፡ እባቡ በእጁ ላይ እንደ ገና በትር ሆነ፡፡ 5 «ይህ የሆነው የአባቶቻቸው አምላክ፣ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክ፣ የያዕቆብ አምላክ እግዚአብሔር የተገለጠልህ መሆኑን እነዲያምኑ ነው፡፡» 6 ደግሞም እግዚአብሔር ሙሴን፣ «እጅህን በብትህ ውስጥ አግባ» አለው፡፡ እጁን ሲያወጣው እነሆ፣ እንደ በረዶ ነጽቶ ለምጽ ሆኖአል፡፡ 7 እግዚአብሔር፣ «እጅህን እንደ ገና በብብትህ ውስጥ አግባ» አለው፡፡ ሙሴም እጁን በብብቱ ውስጥ አገባ፣ ከብብቱ ሲወጣውም እንደ ሌላው ሰውነቱ ጤናማ ሆኖ አየው፡፡ 8 እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፤ «ባያምኑህ፣ የመጀመሪያውን የተአምር ምልክት ባይቀበሉ ወይም ባያምኑበት፣ ሁለተኛውን ያምናሉ፡፡ 9 እነዚህን ሁለት የተአምር ምልክቶች ባያምኑም እንኳ፣ ወይም ባይሰሙህ፣ ከወንዙ ጥቂት ውሀ ወስደህ በደረቁ መሬት ላይ አፍስሰው፡፡ ያፈሰስኸውም ውሀ በደረቁ መሬት ላይ ደም ይሆናል፡፡» 10 እግዚአብሔርን፣ «ጌታ ሆይ፣ በፊትም፣ አንተ ለባሪያህ ከተናገርህ ወዲህም ርቱዕ አንደበት ያለኝ አይደለሁም፡፡ ኮልታፋና ንግግር የማልችል ሰው ነኝ» አለው፡፡ 11 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ አለው፤ «የሰውን አንደበት የፈጠረ ማን ነው? ሰውን ዲዳ ወይም ደንቈሮ ወይም እንዲያይ ወይም እንዲታወር የሚያደርግስ ማን ነው? እኔ እግዚአብሔር አይደለምን? 12 አሁን ሂድ፤ እኔም ከአፍህ ጋር እሆናለሁ፤ ምን እንደምትናገርም አስተምርሃለሁ፡፡» 13 ሙሴ ግን፣ «ጌታ ሆይ፣ እባክህ ልትልከው የምትፈልገውን ሌላ ሰው ላክ» አለ፡፡ 14 በኋላ እግዚአብሔር ሙሴን ተቈጣው፡፡ እንዲህም አለው፤ «ሌዋዊው ወንድምህ አሮንስ? እርሱ በሚገባ መናገር እንደሚችል ዐውቃለሁ፡፡ እንዲያውም ከአንተ ጋር ለመገናኘት እየመጣ ነውና ሲያይህ በልቡ ደስ ይሰኛል፡፡ 15 አንተ ለእርሱ ትናገራለህ፤ የሚናገራቸውንም ቃላት በአፉ ውስጥ ታስቀምጣለህ፡፡ እኔ በአፍህና በአፉ እሆናለሁ፣ ምን እነደምታደርጉም አሳያችኋለሁ፡፡ 16 ለሕዝቡ ይናገርልሃል፡፡ እርሱ የአንተ አፍ ይሆናል፤ አንተም ለእርሱ እንደ እኔ፣ አምላክ ትሆነዋህ፡፡ 17 ይህን በትር በእጅህ ትይዛለህ፣ በእርሱም ተአምራትን ታደርጋለህ፡፡» 18 ሙሴም ወደ ዐማቱ ወደ የቶር ተመልሶ ሄደ፤ «ግብፅ ውስጥ ወዳሉት ዘመዶቼ ተመልሼ እንድሄድና አሁንም ድረስ በሕይወት መኖራቸውን እንዳይ ፍቀድልኝ» አለው፡፡ ዮቶርም ሙሴን፣ «በሰላም ሂድ» አለው፡፡ 19 ምድያም ውስጥ እያለ እግዚአብሔር «ሂድ፣ ወደ ግብፅ ተመለሰ፤ ሊገድሉህ የሚፈልጉ ሰዎች ሁሉ ሞተዋል» አለው፡፡ 20 መሴም ሚስቱንና ልጆቹን ይዞ፣ በአህያ ላይም አስቀምጦ ወደ ግብፅ ተመለሰ፤ የእግዚአብሔርን በትርም በእጁ ይዞ ነበር፡፡ 21 ሙሴን እንዲህ አለው፤ «ወደ ግብፅ ተመልሰህ ስትሄድ፣ በእጅህ ያስቀመጥኋቸውን ተአምራት ሁሉ በፈርዖን ፊት እንደምታደርግ ዐስብ፡፡ ነገር ግን እኔ ልቡን አደነድነዋለሁ፤ ሕዝቡ እንዲሄዱም አይፈቅድም፡፡ 22 እንዲህ ብለህ ንገረው፤ «እግዚአብሔር እየተናገረ ያለው ይህን ነው፤ እስራኤል ልጄ፣ በኵሬ ነው፤ 23 «እንዲያመልከኝ ልጄን ልቀቅ ብዬ እነግርሃለሁ፡፡» ነገር ግን ለመልቀቅ እምቢ ስላለህ፣ በኵር ልጅህን እገድላለሁ፡፡» 24 ላይ ለምሽቱ ዐርፈው ሳለ፣ እግዚአብሔር ሙሴን አግንኝቶ ሊገድለው ነበር፡፡ 25 ግን ስለታም ቢላዋ ይዛ የልጇን ሸለፈት ገረዘች፤ እግሩንም አስነካችው፡፡ ከዚያም በኋላ «አንተ ለእኔ በእውነት የደም ሙሽራዬ ነህ» አለች፡፡ 26 እግዚአብሔር ሙሴን ተወው፡፡ «አንተ የደም ሙሽራ ነህ» ብላ የተናገረችው በግርዘቱ ምክንያት ነው፡፡ 27 አሮንን፣ «ወደ ምድረ በዳ ሂድና ከሙሴ ጋር ተገናኝ» አለው፡፡ አሮን ሄደ፣ ሙሴንም በእግዚአብሔር ተራራ ላይ አግኝቶ ሳመው፡፡ 28 እንዲናገር የላከለትን የእግዚአብሔር ቃሎች ሁሉና እንዲፈጽማቸው ያዘዘውን ተአምራት በሙሉ ለአሮን ነገረው፡፡ 29 በኋላ ሙሴና አሮን ሄደው የእስራኤልን ሽማግሌዎች ሁሉ በአንድነት ሰበሰቡ፡፡ 30 እግዚአብሔር ተአምራትም በሕዝቡ ፊት አሳየ፡፡ 31 አመኑ፡፡ እግዚአብሔር እስራኤላውያንን የጐበኛቸውና የደረሰባቸውን ጭቈና የተመለከተ መሆኑን ሲሰሙም ሰገዱ፣ አመለኩትም፡፡



Exodus 4:1

• እነሆ አያምኑኝም ቃሌንም አይሰሙም

ምንም እንኳን ሙሴ በእግዚአብሔር (በያህዌ) ብያምንም በእርሱ አልታመነም። ይህ የሚያሳየው ሙሴ የእግዚአብሔርን ማንነት ያለመረዳቱን ያሳያል። ሙሴ የተረዳው እርሱ እንዲያደርግ የተጠየቃቸው ነገሮች በእርሱ ሀይል የሚሆኑ መስሎት ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር እየጠየቀ ያለው “በእርሱ እንዲታመንና ሀይሉን እንዲያስተውል ነው።

Exodus 4:4

• እጅህን ዘርግተህ ጅራትዋን ያዝ

እጅህን ዘርጋና ጅራቷን ይዘህ አንሣት

• በእጁም ውስጥ በትር ሆነች

ሙሴም እጁን ዘርግቶ ሲይዛት እባቧ ተለውጣ በእጁ ላይ እንደ ገና በትር ሆነች ማለት ነው

Exodus 4:6

• እነሆ

በዚህ ክፍል የዚህ ቃል ጥቅም ቃለ አጋኖ ለመፍጠር እና መደነቅን ለማሳየት ነው

• እንደ በረዶ ለምጽ ሆነች

እንደ በረዶ ነጭ ሆነ የሚል ሲሆን ተነጻጻሪ ዘይቤ ነው

Exodus 4:8

• ከወንዙ ውኃን ውሰድ

ይህ ወንዝ የአባይ ወንዝ ወይም በእንግሊዘኛው ናይል ወንዝ የሚንለው ነው።

Exodus 4:10

• አፌ ኮልታፋ

ደህና አድርጎ መናገር የማይችል ወይም አንደበቴ ርቱዕ ያልሆነ ሰው ማለት ነው

• ምላሴም ጸያፍ የሆነ ሰው ነኝ

አንደበቱ የሚኮላተፍና አጥርቶ መናገር የማይችል ሰው ማለት ነው። ሙሴ ይህን የተናገረው አጥርቶ መናገር የማይችል ሰው መሆኑን ለመግለጽ ሲፈልግ ነው።

• ምላሴም ጸያፍ

ኮልታፋና ተናግሮ ለማሳመን አቅም የሚያንሰው መሆኑን ያሳያል (ምትካዊ ዘይቤ)

• የሰውን አፍ የፈጠረ ማን ነው?

እግዚአብሔር (ያህዌ) ይህን ጥያቄ ሲጠይቅ ሰዎች መናገር እንዲችሉ አድርጎ የፈጠረውና ለመናገርም አፍ የፈጠረው እርሱ ራሱ መሆኑን ለማጽናት ፈልጎ ነው (አጋናኝ ዘይቤ)

• ዲዳስ ደንቆሮስ የሚያይስ ዕውርስ ያደረገ ማን ነው?

እግዚአብሔር (ያህዌ) ይህን ጥያቄ የጠየቀው ሰዎች መናገርና መስማት እንዲችሉ የሚያደርገው ራሱ እንደሆነ ለማሳየት ነው (አጋናኝ ጥያቄ)

• እኔ እግዚአብሔር አይደለሁምን?

እግዚአብሔር ይህን ጥያቄ ሲጠይቅ ሁሉን ነገር የሚወስነው ራሱ እግዚአብሔር መሆኑን ለማጽናት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ይህን ሁሉ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር አይደለሁምን? (አጋናኝ ጥያቄ) ወይም ይህን ሁሉ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር ነኝ።

• እኔም ከአፍህ ጋር እሆናለሁ

“አፍ” የሚለው ቃል የሙሴ የመናገር ችሎታውን ለማሳየት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “የመናገር ችሎታ ለአንተ እሰጣለሁኝ” ወይም “መናገር እንድትችል አደርጋለሁ”

Exodus 4:14

• የእግዚአብሔርም ቁጣ በሙሴ ላይ ነደደ

“ቁጣ” እንደ እሳት የመንደድ ባህርይ እንዳለው ተደርጎ የቀረበው ተለዋጭ ዘይቤ ነው። እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ ላይ እጅግ ተቆጣ።

• ሌዋዊው ወንድምህ አሮን

ሌዋዊ የሆነው ወንድምህ አሮን/ከሌዊ ነገድ የሆነው ወንድምህ አሮን

• ባየህም ጊዜ በልቡ ደስ ይለዋል

“በልቡ” የሚለው ቃል የአንድ ሰው ውስጣዊ ሀሳቡንና ስሜቱን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፡ አንተን በሚያይበት ጊዜ በጣም ደስ ይለዋል (ምትካዊ ዘይቤ)

• ቃሉንም በአፉ ታደርገዋለህ

ቃሉን በአፉ ታደርገዋል የሚለው ሀረግ አንድን ነገር በአንድ ሰው አፍ ውስጥ እንደማኖር/እንደማስቀመጥ ይታይ ይሆናል። አማራጭ ትርጉም፦ “እርሱ መናገር ያለበትን መልዕክት ይሰጠዋል/ያቀርብለታል”

• እኔ ከአፍህና ከአፉ ጋር እሆናለሁ

ከ “አፍህና ከአፉ” ጋር የሚሉ ቃላት የሚያሳዩት ሁለቱም የሚጠቀሙትን የቃላት ምርጫና አጠቃቀም ይመለከታል። ሙሴና አሮን መልዕክታቸውን ለማስተላለፍ ተገቢ የሆነ ቃላት ይመርጣሉ ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ መልዕክታችሁን ለማስተላለፍ የሚያስችላችሁን ተገቢ ቃል እሰጣችኋለሁ (ምትካዊ ዘይቤ)

• እርሱ አፍ ይሆንልሃል (ምትካዊ ዘይቤ)

ይህ አባባል የሚያሳየን አሮን የሚናገረው ሙሴ የተናገረውን መልዕክት መሆኑን ነው።

• አንተም በእግዚአብሔር ፈንታ ትሆንለታለህ

እግዚአብሔር በሙሴ ላይ እንዳለው ዓይነት ሥልጣን ሙሴ በአሮን ላይ ይኖረዋል ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “እንተ ለአሮን ሲትናገር እኔ እግዚአብሔር ለአንተ (ለሙሴ) በተናገረው ስልጣን ለአሮን ትናገራለህ”

Exodus 4:18

• ወደ አማቱ ወደ ዮቶር ተመለሰ

ሙሴ ወደ ሚስቱ አባት ወይም ወደ አማቹ ወደ ዮቶር ተመለሰ ማለት ነው

Exodus 4:21

• እኔ ግን ልቡን አጸናዋለሁ

እኔ ልቡን አጸናዋለሁ ማለት አበረታታዋለሁ ወይም ድፍረት እሰጠዋለሁ ማለት ሳይሆን ልቡን አደነድነዋለሁ፥ አመጸኛ አደርገዋለሁ፥ እንዳይታዘዝና እንዳይሰማ አደርገዋለሁ ማለት ነው (ምትካዊና ንጽጽራዊ ዘይቤ)።

• እስራኤል የበኩር ልጄ ነው

እስራኤል የሚለው ቃል መላውን የእስራኤል ህዝብ የሚወክል ቃል ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “የእስራኤል ህዝብ የእኔ ልጆች” ናቸው።

• የበኩር ልጄ ነው

የእስራኤል ህዝብ የእግዚአብሔር ልጅ ብቻ ሳይሆን ደስታና ኩራት የሆነ የእግዚአብሔር ልጅ ነው (ተለዋጭ ዘይቤ)።

Exodus 4:24

• በመንገድ ላይ ባደረበት ስፍራ እግዚአብሔር ተገናኘው፥ ሊገድለውም ፈለገ

የዚህ ትርጉም በትክክል ባይታወቅም ምናልባት ሙሴ ልጁን ባለመገረዙ ምክንያት ሊሆን ይችላል።

• ሲፓራም ሚስቱ

የሙሴ ሚስት ስሟ ሲፖራ ወይም በዕብራይስጡ ጽፖራ ነው።

• ባልጩት

የተፈጥሮ ስለት ያለው ለመቁረጥ የሚያገለግል የባልጩት ድንጋይ

• ወደ እግሩም ጣለችው

ይህ “ወደ እግሩም ጣለችው” የሚለው ሀረግ ሁለት ዋና ዋና የትርጉም አመለካከቶች አሉት። 1) ልጁ መገረዙን ለማመልከት በእግሩ ላይ የደም ምልክት እንድኖር ስትፈልግ እናቱ የቆረጠችውን ሸለፈት በልጁ እግር ላይ መጣሏን፤ 2) “እግር” የሚለው ቃል በእስራኤላውያን ዘንድ የአይነኬ ዘይቤ አገላለጽ በመሆኑ ወደ ሙሴ የመዋለጃ ብልት ላይ ጣለችው የሚል አመለካከትም አለው።

• አንተ ለእኔ የደም ሙሽራ ነህ

የዚህ ሀረግ ፍቺው ወይም መልዕክት ግልጽ አይደለም። እንደዚህ ዓይነት ንግግር በጊዜው በእስራኤል ታሪክ የሚታወቅ ልሆን ይችላል። አማራጭ ትርጉም፦ “በዚህ ደም ምክንያት አንተ ከእኔ ጋር ግንኙነት አለ” ወይም “በዚህ ደም ምክንያት አንተ ለእኔ ባሌ ነህ”

Exodus 4:27

• እግዚአብሔርም አሮንን

በዚህ ክፍል የታሪኩን አዲስ ጀማሮ ለማመልከት የሚረዳ አንድ አገናኝ ቃል መጠቀም ጥሩ ነው። ለምሳሌ፦ “በዚህን ጊዜ” ብሎ መቀጠል ይቻላል።

• በእግዚአብሔር ተራራ ተገናኘው

ይህ በሲና የሚገኘው ተራራ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን በትክክል የትኛው ተራራ እንደሆነ አይናገርም።

• እግዚአብሔር በእርሱ ዘንድ የላከውን ቃል ሁሉ

በእርሱ ዘንድ የሚለው ቃል በሙሴ በኩል የሚለውን ፍቺ ይይዛል።

Exodus 4:29

• ጭንቀታቸውንም አየ

እግዚአብሔር እስርኤላውያንን አየ ወይም ለእነርሱ አሰበ የሚል ነው።

• አጎነበሱ ሰገዱም

ተንበርክከው ሰገዱ የሚል ነው


Chapter 5

1 እነዚህ ነገሮች ከሆኑ በኋላ፣ ሙሴና አሮን ወደ ፈርዖን ሄደው፣ እንደዚህ አሉ፤ «የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር የሚለው ይህ ነው፡- ‹በምድረ በዳው ለእኔ በዓል እንዲያደርጉ ሕዝቤን ልቀቅ፡፡»› 2 ፈርዖንም፣ «እግዚአብሔር ማን ነው? ቃሉን የምሰማው፣ እስራኤልንስ የምለቅ ለምንድን ነው? እግዚአብሔርን አላውቀውም፤ እስራኤልንም አልለቅም» አለ፡፡ 3 ሙሴና አሮንም፣ «የዕብራውያን አምላክ ከእኛ ጋር ተገናኝቶአል፡፡ በመቅሠፍትና በሰይፍ እንዳይመታን፣ ወደ ምድረ በዳው የሦስት ቀን ጕዞ እንድናደርግና ለእግዚአብሔር እንድንሠዋ ፍቀድልን» አሉት፡፡ 4 የግብፅ ንጉሥ ግን፣ «አንተ ሙሴ አንተም አሮን! ሕዝቡን ሥራቸውን አስፈትታችሁ የምትወስዷቸው ለምንድን ነው? ወደ ሥራችሁ ሂዱ» አላቸው፡፡ 5 እንዲህ አላቸው፤ «በምድራችን አሁን ብዙ ዕብራውያን አሉ፤ እናንተም ሥራ ታስፈቷቸዋላችሁ፡፡» 6 በዚያው ቀን ፈርዖን ለሕዝቡ አሠሪዎችና ተቈጣጣሪዎች ትእዛዝ ሰጠ፡፡ እንዲህም አለ፤ 7 «እንደ ቀድሞው፣ ከእንግዲህ ወዲያ ለሸክላ ሥራ ጭድ አታቅርቡ፡፡ እነርሱ ራሳቸው ይሂዱና ጭድ ይሰብስቡ፡፡ 8 ሆኖም በፊት የሚሠሩትን አንድ ዐይነት የሸክላ ቊጥር አሁንም ሠርተው እንዲያቀርቡ ማድረግ አለባችሁ፡፡ ከዚያ ያነሰ አትቀበሉ፤ ምክንያቱም ሰነፎች ናቸው፡፡ ‹እንሂድ ፍቀድልንና ለአምላካችን እንሠዋ› እያሉ የሚጮኹትም ለዚህ ነው፡፡ 9 እንዲተጉና ለማይረባ ንግግር ትኵረት እንዳይሰጡ ሥራውን ጨምራችሁ አክብዱባቸው፡፡» 10 ስለዚህ የሕዝቡ አሠሪ አለቆችና ተቈጣጣሪዎች ወጥተው ሄዱ፤ ለሕዝቡም ነገሯቸው፡፡ እንዲህም አሉ፤ «ፈርዖን የሚለው ይህ ነው፡- ‹ከእንግዲህ ወዲያ ምንም ጭድ አልሰጣችሁም፡፡ 11 ሂዱና ማግኘት ከምትችሉበት ፈልጋችሁ አምጡ፤ የሥራችሁ መጠንም አይቀላለም፡፡» 12 ሕዝቡ በጭድ ፈንታ ገለባ ለመሰብሰብ በግብፅ ምድር ሁሉ ተሠራጩ፡፡ 13 አለቆቹ፣ «ጭድ በሚቀርብላችሁ ጊዜ የምትሠሩትን ሥራችሁን ጨርሱ» ይሏቸውና ያስጠነቅቋቸው ነበር፡፡» 14 ፈርዖን የመደባቸው አሠሪ አለቆች የሠራተኞች ተቈጣጣሪ ያደረጓቸውን እስራኤላውያን ኀላፊዎች ገረፏቸው፡፡ አሠሪ አለቆቹ፣ «በፊት ታደርጉት እንደ ነበረው፣ ትናንትናም ዛሬም የሚጠበቅባችሁን ሸክላ በሙሉ ሠርታችሁ ያላቀረባችሁ ለምንድን ነው?» እያሉ ይጠይቋቸው ነበር፡፡ 15 እስራኤላውያን ተቈጣጣሪዎቹም ወደ ፈርዖን መጥተው አቤቱታ አቀረቡ፡፡ እንደዚህም አሉት፤ «ባሪያዎችህን በዚህ መንገድ ለምን እንድንኖር ታደርጋለህ? 16 ጭድ አይሰጡንም፤ ነገር ግን አሁንም ‹ሸክላ ሥሩ!› ይሉናል፡፡ እኛ ባሪያዎችህ ተገርፈናልም፤ ስሕተቱ ግን የገዛ ሕዝብህ ነው፡፡» 17 ግን እንዲህ አለ፤ «እናንተ ሰነፎች! እናንተ ሰነፎች! ‹ለእግዚአብሔር እንድንሠዋ ፍቀድልን› ትላላችሁ፡፡ 18 ወደ ሥራ ተመለሱ፡፡ አንዳችም ጭድ አይሰጣችሁም፤ ነገር ግን አሁንም ያንኑ የሸክላ ቊጥር መሥራት አለባችሁ፡፡» 19 «የየቀኑን የሸክላ ቊጥር መቀነስ የለባችሁም» የሚለው ሲነገራቸው፣ እስራኤላውያን ተቈጣጣሪዎች ችግር ውስጥ እንደ ነበሩ አስተዋሉ፡፡ 20 ከፈርዖን ዘንድ ሲወጡ፣ ከቤተ መንግሥቱ ውጭ ቆመው ከነበሩት ከሙሴና ከአሮን ጋር ተገናኙ፡፡ 21 ለሙሴና ለአሮንም እንዲህ አሏቸው፣ «እግዚአብሔር ይይላችሁ፣ ይፍረድባችሁም፤ ምክንያቱም በፈርዖንና በአገልጋዮቹ ፊት አስጸያፊዎች እንድንሆን አድርጋችሁናል፡፡» 22 ወደ እግዚአብሔር ተመልሶ፣ «ጌታ ሆይ፣ በዚህ ሕዝብ ላይ መከራ እንዲደርስበት ያደረግህ ለምንድን ነው? እኔንስ ቀድሞውኑ ለምን ላክኸኝ? 23 ስም ልነግረው ወደ ፈርዖን ከመጣሁበት ጊዜ ጀምሮ፣ በዚህ ሕዝብ ላይ መከራ አምጥቶአል፤ አንተም ሕዝብህን ከቶ ነጻ አላወጣኸውም» አለው፡፡



Exodus 5:1

• ከዚህም በኋላ

በትረካ ውስጥ “ከዚህ በኋላ” የሚለው አገናኝ ሀረግ አንድ ዋና ሀሳብ ከተነገረ በኋላ ቀጣይ የትረካው አካል መከተሉን ያመለክታል። ይሁን እንጂ ሙሴና አሮን ወደ ፈርዖን ተመልሰው ለመሄድ ምን ያህል ጊዜ እንደወሰደባቸው ግልጽ አይደለም።

• በዓል ያደርግልኝ ዘንድ

እግዚአብሔርን በማምለክ የአግዚአብሔር በዓል እንዲያደርጉ ወይም እንዲያከብሩ ማለት ነው

• እግዚአብሔር ማን ነው?

ይህ አጋናኝ ጥያቄ የሚያሳየው ፈርዖን እግዚአብሔር እውነተኛ እና ልታወቅ የሚገባ አምላክ መሆኑን ለማወቅ አለመፈለጉን ወይም አለማወቁን አመልካች ነው። በመደበኛ ዐረፍተ ነገር ሲጻፍ፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) ማን እንደሆነ አላውቅም ማለቱ ነው።

• የእርሱን ትእዛዝ ሰምቼ

የእርሱን ድምጽ/ትዕዛዝ ሰምቼ የሚለው እግዚአብሔር የሚናገረውን ቃል ሰምቼ የሚል ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እርሱ/እግዚአብሔር የሚለውን ሰምቼ

Exodus 5:3

• የዕብራውያን አምላክ

ይህ ቃል “የእስራኤላውያን አምላክ ወይም ያህዌ” የሚለውን የሚገልጽ ነው

• ቸነፈር ወይም ሰይፍ እንዳይጥልብን

ይህ ሀረግ እግዚአብሔር በሽታ ሲልክብን ወይም ጦርነት ሲያስነሳብን ወይም ጠላት ሲልክብን ማለት ነው።

• ሕዝቡን ለምን ሥራቸውን ታስተዋላችሁ?

ፈርዖን ይህን አጋናኝ ጥያቄ ሙሴንና አሮንን ሲጠይቅ እስራኤላውያን ሥራ እንዳይሰሩ እያደረጉ ነው ብሎ ስላሰበና በእነርሱ ላይ መቆጣቱን ለመግለጽ ነው። እማራጭ ትርጉም፦ “ህዝቡ ሥራ እንዳይሰራ አታደርጉ ወይም ሥራ አትከለክሉ ወይም ሥራ አታስፈቱ”

Exodus 5:6

• አስገባሪዎች ሹማምቶቹንም

ግብጻውያን አሠሪዎችና የእስራኤላውያን ሠራተኞች አለቆችን የሚመለከት ነው

• ለጡብ ሥራ ገለባ ለሕዝቡ አትስጡ

ይህን እንዳያደርጉ የተነገራቸው አስገባሪዎችና ሹማምቶችን ነው። “አትስጡ” የሚለው የወል ስም ስለሆነ አሰሪ አለቆችን ይመለከታል።

Exodus 5:10

• አስገባሪዎች ሹማምቶቹንም

ግብጻውያን አሠሪዎችና የእስራኤላውያን ሠራተኞች አለቆችን የሚመለከት ነው (ዘጸአት 1፡11 ተመለከት)

• ገለባ አልሰጣችሁም

“አልሰጣችሁም” ሲል ለእናንተ የሚለውን የወል ስም የሚገልጽ ሲሆን እስራኤላውያንን የሚመለከት ነው።

• እናንተ ሂዱ

ግብጻውያን ገለባ በመሰብሰብ ሥራ እስራኤላውያንን አያግዙአችሁም ማለት ነው። ራሳቸው ለገለባ ፍለጋ ይሄዳሉ ማለት ነው።

• ከሥራችሁ ግን ምንም አይጎድልም

ይህን አገላለጽ በሌላ መልክ ሲገለጽ፦ ከዚህ በፊት በምትሰሩት ጡብ ልክ ሥራችሁን ሰርታችሁ ታቀርባላችሁ ማለት ነው።

Exodus 5:12

• በግብፅ ምድር ሁሉ ተበተኑ

የተሰጣቸውን ወይም የተጣለባቸውን ሥራ ለመስራት እስራኤላውያን በግብጽ ምድር መሰራጨታቸውን ያመለክታል። አማራጭ ትርጉም፦ በግብጽ ምድር በሁሉም አከባቢዎች እስራኤላውያን ተበተኑ። (ግነታዊና ጥቅል ዘይቤያዊ አነጋገር ተመልከት)

• ገለባ

የስንዴ፥ የገብስ፥ የጤፍ፥ እና የመሳሰሉት የሰብል ዓይነቶች ከአጨዳ ወይም ከውቂያ በኋላ የቀረው ክፍል ነው።

አስገባሪዎች

ግብጻውያን አሠሪዎችና የእስራኤላውያን ሠራተኞች አለቆችን የሚመለከት ነው (ዘጸአት 1፡11 ተመለከት)

• ቀድሞ ታደርጉ እንደ ነበራችሁ ትናንትናና ዛሬ የተቆጠረውን ጡብ ስለ ምን አትጨርሱም?

ግብጻውያን አሰሪዎቻቸው ይህን ጥያቄ እስራኤላውያንን የጠየቁት የምጠበቅባቸውን ጡብ ሰርተው ለማቅረብ ባለመቻላቸው ተቆጥተውባቸው ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ከዚህ ከደም እንደምታደርጉት ትናንትም ይሁን ዛሬ የሚጠበቅባችሁን ጡብ ሰርታችሁ ማቅረብ አልቻላችሁም (አጋናኝ ጥያቄ)።

Exodus 5:15

• ግድፈቱ ግን በአንተ ሕዝብ ላይ ነው ብለው ጮሁ

ጥፋቱ ወይም ስህተቱ የገዛ ሰዎችህ ነው እንጂ የእኛ አይደለም ብለው አቤቱታ አቀረቡ

• የጡቡንም ሥራ እንድንሠራ ያዝዙናል

“ያዝዙናል” የሚለው ቃል ግብጻውያን አሰሪዎችን የሚመለከት ነው

Exodus 5:19

• በፈርዖንና በባሪያዎቹ ፊት ሽታችንን አግምታችሁታልና

ምክንያቱም እናንተ (ሙሴና አሮን) በንጉሡ በፈርዖንና በመኳንንቱ ዘንድ እጅግ እንድንጠላ አድርጋችሁናል (ተለዋጭ ዘይቤ)

• ይገድሉንም ዘንድ ሰይፍን በእጃቸው ሰጥታችኋቸዋልና

ምክንያቱም እነርሱ እኛን እንዲገድሉ ምክንያት በመሆናችሁ ሰይፍን በእጃቸው ሰጥታችኋቸዋል። ሰይፍ የሚወከለው ያጠፉአቸው ዘንድ ምቹ አጋጣሚ መፈጠሩን ለማመልከት ነው።

Exodus 5:22

• ስለ ምን ይህን ሕዝብ አስከፋህ? (አጋናኝ ጥያቄ)

ይህ አጋናኝ ጥያቄ የሚመለከተው ሙሴ በእስራሴላውያን መበደልና ርህራሄ የለሽ ተግባራቸው የተከፋ መሆኑን ያሳያል። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር ሆይ በእስራኤላውያን ላይ በደረሰው ነገር በጣም አዝናለሁ

• ስለ ምንስ ላክኸኝ? (አጋናኝ ጥያቄ)

ሙሴ እስራኤላውያንን ነጻ እንዲያወጣ በመላኩ ማዘኑን የሚያመለክት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ወደዚህ ስፍራ ባትልከኝ እመርጥ ነበር።

• በስምህ እናገር ዘንድ

“በስምህ” የሚለው የእግዚአብሔር መልዕክት ለማማመልከት ነው


Chapter 6

1 ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር ሙሴን፣ «በፈርዖን ላይ የማደርገውን አሁን ታያለህ፡፡ ከጽኑዕ እጄ የተነሣ ሕዝቡን ይለቃቸዋልና፣ ይህን ታያለህ፡፡ ከጽኑዕ እጄ የተነሣ ሕዝቡን ከምድሩ ያስወጣቸዋል» አለው፡፡ 2 ለሙሴ እንዲህ አለው፤ «እኔ እግዚአብሔር ነኝ፡፡ 3 እኔ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅ፣ ለያዕቆብ ሁሉን እንደሚችል አምላክ ተገለጥሁላቸው፤ ነገር ግን በስሜ፣ በእግዚአብሔር ለእነርሱ አልታወቅሁላቸውም ነበር፡፡ 4 የተሰደዱባትን፣ በእንግድነት የኖሩባትን የከነዓንን ምድር ልሰጣቸው፣ ከእነርሱ ጋር ኪዳን አጽንቻለሁ፡፡ 5 ደግሞም ግብፃውያን ባሪያ ያደረጓቸውን የአስራኤላውያንን ጩኸት ሰምቻለሁ፤ ኪዳኔንም አስታውሻለሁ፡፡ 6 ስለዚህ ለእስራኤላውያን እንዲህ በላቸው፤ ‹እኔ እግዚአብሔር ነኝ፡፡ በግብፃውያን ሥር ከምትኖሩባት ባርነት እታደጋችኋለሁ፤ ከአገዛዛቸውም ነፃ አወጣችኋለሁ፡፡ በታላቅ ፍርድና ኀይሌን በማሳየት እታደጋችኋለሁ፡፡ 7 አድርጌ ወደ ራሴ እወስዳችኋለሁ፤ እኔም አምላካችሁ እሆናለሁ፡፡ ግብፃውያን ከጫኑባችሁ ባርነት ነፃ ያወጣኋችሁ አምላካችሁ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ፡፡ 8 ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ልሰጥ ቃል ወደገባሁባት ምድር አስገባችኋለሁ፡፡ ምድሪቱን ርስት አድርጌ እሰጣችኋለሁ፡፡ እኔ እግዚአብሔር ነኝ፡፡» 9 ይህን ለእስራኤላውያን በነገራቸው ጊዜ፣ በአስከፊው ባርነታቸው ተስፋ ከመቊረጣቸው የተነሣ አላደመጡትም፡፡ 10 ሙሴን እንዲህ አለው፤ 11 ሂድና ለግብፅ ንጉሥ ለፈርዖን የእስራኤልን ሕዝብ ከምድሩ እንዲለቅ ንገረው፡፡ 12 ሙሴም እግዚአብሔርን፣ «ተብታባ በመሆኔ እስራኤላውያን ካልሰሙኝ፣ ፈርዖን እንዴት ይሰማኛል? 13 እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን አናገራቸው፡፡ እስራኤላውያን ከግብፅ ምድር እንዲያስወጡ ስለ ግብፅ ንጉሥ ስለ ፈርዖንና ስለ እስራኤላውያንም ትእዛዝ ሰጣቸው፡፡ 14 የአባቶቻቸውም ቤት አለቆች እነዚህ ነበሩ፤ የእስራኤል በኵር ልጅ የሮቤል ልጆች ሄኖኅ፣ ፈሉስ፣ አስሮንና ከርሚ ነበሩ፡፡ እነዚህ የሮቤል ነገድ ናቸው፡፡ 15 የስምዖን ልጆች ይሙኤል፣ ያሚን፣ ኦሃድ፣ ያኪን፣ ዱሐርና የከነዓናዊቷ ሴት ልጅ ሳኡል ነበሩ፡፡ እነዚህ የስምዖን ነገድ አባቶች ናቸው፡፡ 16 የሌዊ ልጆች ስሞች ከትውልዶቻቸው ጋር እነዚህ ናቸው፤ ጌድሶን፣ ቀዓትና ሜራሪ ነበሩ፡፡ ሌዊ መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፡፡ 17 የጌድሶን ልጆች ሉቤኒና ሰሜኢ ነበሩ፡፡ 18 የቀዓት ልጆች እንበረም፣ ይሰዓር፣ ኬብሮንና ዑዝኤል ነበሩ፡፡ ቀዓት መቶ ሠላሳ ሦስት ዓመት ኖረ፡፡ 19 የሜራሪ ልጆች ሞሖሊና ሙሲ ነበሩ፡፡ እነዚህ በትውልዶቻቸው መሠረት፣ የሌዋውያን የነገድ አባቶች ሆኑ፡፡ 20 የአባቱን እኅት ዮካብድን አገባ፤ እርሷምአሮንንና ሙሴን ወለደችለት፡፡ እንበረም መቶ ሠላሳ ሰባት ዓመት ኖሮ ሞተ፡፡ 21 የይስዓር ልጆች ቆሬ፣ ናፌግና ዝክሪ ነበሩ፡፡ 22 ልጆች ሚሳኤል፣ ኤልዳፋንና ሥትሪ ነበሩ፡፡ 23 የአሚካዳብን ልጅ፣ የነኦሶንን እኅት ኤልሳቤጥን አገባ፡፡ እርሷም ናዳብንና አብዩድን፣ አልዓዛርንና ኢተምርን ወለደችለት፡፡ 24 የቆሬ ልጆች አሴር፣ ሕልቃናና አብያሳፍ ነበሩ፡፡ እነዚህ የቆሬ ነገድ አባቶች ናቸው፡፡ 25 ልጅ አልዓር ከፏትኤል ልጆች አንዲቱን አገባ፡፡ እርሷም ፊንሐስን ወለደችለት፡፡ እነዚህ በየትውልዶቻቸው የሌዋውያን አባቶች ቤቶች አለቆች ናቸው፡፡ 26 ሁለት ሰዎች፣ «እስራኤላውያንን በየተዋጊ ሰራዊታቸው ከግብፅ ምድር አውጡ» ብሎ እግዚአብሔር ያዘዛቸው አሮንና ሙሴ ነበሩ፡፡ 27 ሙሴ እስራኤላውያንን ከግብፅ ለማውጣት እንዲፈቅድላቸው ለግብፅ ንጉሥ ለፈርዖን ተናገሩ፡፡ እነዚህ ሙሴና አሮን እነዚያው ራሳቸው ነበሩ፡፡ 28 እግዚአብሔር በግብፅ ውስጥ ሙሴን ባናገረው ጊዜ፣ 29 «እኔ እግዚአብሔር ነኝ፡፡ የምነግርህን ሁሉ ለግብፅ ንጉሥ ለፈርዖን ንገረው» አለው፡፡ 30 ግን እግዚአብሔርን፣ «እኔ ተብታባ ነኝ፤ ፈርዖን ታዲያ እንዴት ይሰማኛል? አለው፡፡



Exodus 6:1

• በጸናች እጅ ይለቅቃችኋልና፥ በጸናችም እጅ ከምድሩ አስወጥቶ ይሰድዳቸዋልና (ምትካዊ ዘይቤ)

“የጸናች እጅ” የፈርዖን እጅ ሳይሆን የእግዚአብሔር ሀይል ለማመልከት ነው። “እጅ” ምትካዊ ዘይቤ ስለሆነ የእግዚአብሔርን ሀይል ይመለከታል። አማራጭ ትርጉም፦ “በእግዚአብሔር ሀይል ይለቃቸዋል፤ በሀይሌም ከምድርቱ አስወጥቶ ይሰዳቸዋል”

Exodus 6:2

• ለአብርሃምም ለይስሐቅም ለያዕቆብም ሁሉን እንደሚችል አምላክ ተገለጥሁ

እኔ ራሴን ለአብርሃም፥ ለይስሃቅና ለያዕቆብ አሳየሁ

• ነገር ግን ስሜ እግዚአብሔር አልታወቀላቸውም

ነገር ግን ያህዌ በሚለው ስሜ አላወቁኝም

• የእስራኤልን ልጆች ልቅሶ ሰማሁ

በአማርኛው ቅጅ “ለቅሶ” የሚለው ቃል በዕብራይስጡ ለቅሶ ሳይሆን “ጭንቀትን፥ ሰቆቃን፥ ማቃሰትን፥ መቃተትን” የሚመለከት ነው።

Exodus 6:6

• ለእስራኤል ልጆች እንዲህ በላቸው

ትዕዛዛዊ ንግግር ነው፤ ሙሴ ለእስራኤላውያን እንድነግራቸው ያህዌ ሙሴን ሲያዘው ያሳየናል።

• በተዘረጋ ክንድ በታላቅ ፍርድም እታደጋችኋለሁ

ግብጻውያንን በመቅጣት ወይም በመምታትና ለእስራኤላውያን እውነተኛ ፍርድ በማምጣት ነጻ አወጣችኋለሁ። “የተዘረጋች ክንድ” የሚለው ሀረግ ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን ግብጻውያንን እቀጣለሁ ወይም እፈርድባቸዋለሁ” ማለት ነው።

Exodus 6:8

• ወደ ማልሁባት ምድር አገባችኋለሁ

ተስፋ ወደ ገባሁላቸው ምድር አስገባቸዋለሁ ወይም እሰጣችኋለሁ ብዬ ወደነገርኳቸው ምድር እወስዳችኋለሁ ማለት ነው።

Exodus 6:10

እነሆ የእስራኤል ልጆች አልሰሙኝም፣ እንዴትስ ፈርዖን ይሰማኛል? ይልቁንም እኔ ከንፈረ ቈላፍ ነኝ ብሎ ተናገረ (አጋናኝ ጥያቄ)

ሙሴ ይህን ጥያቄ ሲጠይቅ ሁለት ነገሮችን ተስፋ ያደረገ ይመስላል። 1) ፈርዖን እንደማይሰማኝ ታውቃለህና አታስቸግረኝ ማለቱ ነው 2) እግዚአብሔር የቀድሞ ሀሳቡን ቀይሮ ሙሴን እንዲለቀውና በሙሴ በኩል ልፈጽም ያሰበውን ሀሳብ እንድተው መጠየቁ ነበር። ለዚህ ምክንያት አድርጎ ያቀረበው “እኔ አጥርቼ መናገር የማልችል ኮልታፋ ነኝ” በማለት ነበር። አማራጭ ትርጉም፦ “እስራኤላውያን እስካላመኑ ድረስ ፈርዖንም አያምነኝም”

Exodus 6:14

ዘጸአት 6፡14-25 • የአባታቸውም ቤት አለቆች

የየቤተሰቡ ወይም የየነገድ አለቆች። አማራጭ ትርጉም፦ “የአያቶቻቸው አለቆች ወይም መሪዎች”

• ሄኖክ፥ ፋሉ፥ ሔጽሮን፥ …

የወንዶች ስም ሲሆን የየነገድ ወይም ቅድመ አያቶቻቸው ስም ዝርዝር ነው። ከቁጥር 14-25 ድረስ ባለው ከፍል የተጠቀሱትን የዕብራይስጥ ስሞችንና ቁጥሮችን የመተርጎም ዘዴዎችን አስተውል።

Exodus 6:26

• ከግብፅ ምድር በየሠራዊቶቻቸው የእስራኤልን ልጆች አውጡ

“አንድን ነገድ” ወይም “አንድን ቤተሰብ” በሰልፍ ተራ በተራ መምራትን ያመለክታል። የእስራኤል ሰዎች “ሠራዊት” የተባሉት የጦር ሠራዊት ሆነው ሳይሆን “በየነገዳቸው እንደ ሠራዊት” በሰልፍ መውጣታቸውን ለማመልከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “የእስራኤልን ሕዝብ በየነገዳቸው ከግብጽ ምድር መርታችሁ አውጡ”

Exodus 6:28

• እነሆ እኔ ከንፈረ ቈላፍ ነኝ፣ እንዴትስ ፈርዖን ይሰማኛል?

በዚህ አጋናኝ ጥያቄ ሙሴ የእግዚአብሔርን ሀሳብ ለማስቀየር ያሰበ ይመስላል። እንዲሁም ወደ ፈርዖን ለመሄድ ካለመፈለጉም ሌላ በፈርዖን ድርጊትም ተስፋ የቆረጠ ይመስላል። አማራጭ ትርጉም፦ “እኔ የንግግር ችሎታ ስለሌለኝ ፈርዖን በርግጥ አይስማኝም”


Chapter 7

1 ሙሴን እንዲህ አለው፤ «ልብ በል፤ አንተን ለፈርዖን እንደ አምላክ አድርጌሃለሁ፡፡ ወንድምህ አሮን ነቢይህ ይሆናል፡፡ 2 እንድትናገር ያዘዝሁህን ሁሉ ትናራለህ፡፡ የእስራኤል ሕዝብ ከምድሩ እንዲለቀ፣ ወንድምህ አሮን ለፈርዖን ይናገራል፡፡ 3 ነገር ግን እኔ የፈርዖንን ለብ አደነድነዋሁ፤ የተአምራቴን ብዙ ምልክቶች፣ ብዙ ድንቆችም በግብፅ ምድር አሳያለሁ፡፡ 4 ነገር ግን ፈርዖን አይሰማችሁም፤ ስለዚህ እጄን በግብፅ ላይ አደርጋሁ፤ ሰራዊቱን፣ ሕዝቤን፣ የእስራኤልን ልጆች በታላቅ ፍርድ ከግብፅ ምድር አወጣለሁ፡፡ 5 በግብፅ ላይ ስዘረጋና እስራኤላውያንን ከመካከላቸው ሳወጣ፣ ግብፃውያን እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፡፡» 6 አሮን እንዲሁ አደረጉ፤ እግዚአብሔር ያዘዛቸውን ፈጸሙ፡፡ 7 ባጋገሩት ጊዜ፣ የሙሴ ዕድሜ ሰማንያ፣ የአሮን ደግሞ ሰማንያ ሦስት ነበር፡፡ 8 ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፤ 9 ‹ተአምር አሳዩ› ሲላችሁ፣ አሮንን እንዲህ በለው፤ ‹በትርህን ውሰድና በፈርዖን ፊት ጣለው፤ እባብም ይሀናል፡፡»› 10 ሙሴ አሮን ወደ ፈርዖን ሄደው፣ እግዚአብሔር አዝዞአቸው የነበረውን አደረጉ፡፡ አሮን በትሩን በፈርዖንና በአገልጋዮቹ ፊት ጣለው፤ እባብም ሆነ፡፡ 11 ደግሞ ለጥበበኛ ሰዎቹና ለጠንቋዮቹ ጥሪ አደረገ፡፡ እነርሱም በምትሀታቸው ያንኑ አደረጉ፡፡ 12 እያንዳንዱ ሰው በትሩን ጣለ፤ በትሮቹም እባብ ሆኑ፣ ነገር ግን የአሮን በትር የእነርሱን እባቦች ዋጣቸው፡፡ 13 አስቀድሞ እንደ ተናገረው፣ የፈርዖን ልብ ደነደነ፤ አልሰማምም፡፡ 14 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ «የፈርዖን ልብ ደንድኖአል፤ ሕዘቡም እንዲሄዱ አይፈቅድም፡፡ 15 ወደ ውሃው በሚሄድበት ጊዜ፣ በጠዋት ወደ ፈርዖን ሂድ፡፡ እንዳገኘውም በወንዙ ዳር ቁም፤ ወደ እባብነት ተለውጦ የነበረውን በትርህን ውሰድ፡፡ 16 እንዲህ በለው፤ ‹የዕብራውያን አምላክ እግዚአብሔር ይህን እንድናገር ወደ አንተ ላከኝ፤ «በምድረ በዳ እንዲያመልኩኝ ሕዝቤን ልቀቅ፤ እስካሁን ድረስ አልሰማህም፡፡» 17 የሚናገረው ይህ ነው፤ «እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ በዚህ ታውቃለህ፡፡ የአባይን ወንዝ ውሀ በእጄ በያዝሁት በትር እመታዋለሁ፣ ወንዙም ወደ ደምነት ይለወጣል፡፡ 18 ውስጥ የሚገኙት ዓሦች ይሞታሉ፤ ወንዙ ይከረፋል፡፡ግብፃውያኑም ከወንዙ ውሀ መጠጣት አይችሉም፡፡» 19 ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ለሙሴ እንዲህ አለ፤ አሮንን፣ ‹በትርህን ውሰድና ውሀቸው ደም እንዲሆን፣ በግብፅ ውሀዎች ላይ፣ በወንዞቻቸውም፣ በምንጮቻቸውም፣ በውሀ ማጠራቀሚያዎቻቸውና በኩሬዎቻቸው ሁሉ ላይ እጅህን ዘርጋ ብለህ ንገረው፡፡ በመላው የግብፅ ምድር፣ ከዕንጨትና ከድንጋይ በተሠሩ ውሀ መያዣዎች ያለው ውሀም እንኳ ደም እንዲሆን ይህን አድርግ፡፡»› 20 ሙሴና አሮን እግዚአብሔር እንዳዘዛቸው አደረጉ፡፡ አሮን በትሩን አንሥቶ በፈርዖንና በአገልጋዮቹ ፊት የወንዙን ውሀ መታው፡፡ የወንዙ ውሀ በሙሉ ወደ ደምነት ተለወጠ፡፡ 21 ውስጥ ያለው ዓሣ ሞተ ወንዙም መከርፋት ጀመረ፡፡ ግብፃውያኑ ከወንዙ ውሀ መጠጣት አልቻም፤ ደሙም በግብፅ ምድር በየትኛውም ስፍራ ነበረ፡፡ 22 የግብፅ ጠንቋዮችም በምትሀታቸው ያንኑ ዐይነት ነገር አደረጉ፡፡ ስለዚህ የፈርዖን ልብ ደነደነ፤ እግዚአብሔር ይሆናለ ብሎ ተናግሮት እንደ ተናገረውም ሙሴንና አሮንን ለመስማት እምቢ አለ፡፡ 23 ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ ለዚህ ጉዳይ ትኵረትም እንኳ አልሰጠም፡፡ 24 ግብፃውያኑ ሁሉ በወንዙ ዙሪያ የሚጠጣ ውሀ ለማግኘት ቈፈሩ፤ ነገ ርግን የወንዙን ውሀ መጠጣት አልቻሉም፡፡ 25 እግዚአብሔር ወንዙን ከመታው በኋላ ሰባት ቀን ዐለፈ፡፡



Exodus 7:1

• እይ፥ እኔ ለፈርዖን አምላክ አድርጌሃለሁ

አስተውል፤ ወይም ልብ በል፤ እኔ አንተን ለፈርኦን እንደ አምላክ አድርገሃለሁ።

Exodus 7:3

• እኔም የፈርዖንን ልብ አጸናለሁ

“ልብ” ተብሎ በወካይ ዘይቤ የተገለጠው ራሱን ፈርዖንን ለመግለጽ ነው። የፈርዖንን ልብ ያደነደነው እግዚአብሔር ራሱ እንደሆነ ልብ ይሏል። ስለሆነም ልቡን እግዚአብሔር ስላደነደነው ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም ወይም እምብተኛ ሆነ ማለት ነው። (ምዕራፍ 3፡21 ተመልከት)

• ድንቄንና ተአምራቴን አበዛለሁ

“ድንቅና ታአምር” ሁለቱም ተመሳሳይ ወይም ቅርብ ፍቺ ያላችው ቃላት ናቸው። ታአምር ድርጊቱን ወይም ክስተቱን ሲገልጽ ድንቅ ምልክትን ወይም የክስተቱ ማረጋገጫ የሚመለከት ነው። ሁለቱም ከተፈጥሮ ክስተት ውጪ የሆኑ የእግዚአብሔር አሰራሮች ናቸው።

• እጄንም በግብፅ ላይ አደርጋለሁ

“እጄን” ሲል ለፍርድና ለቅጣት የተዘረጋውን የእግዚአብሔር እጅ እንጂ የማደፋፈር ወይም የማነቃቃት እጅ ማለት አይደለም። አማራጭ ትርጉም፦ ግብጻውያንን በመፍረድ ወይም በመቅጣት ታላቁን ሀይሌን አሳያቸዋለሁ”

Exodus 7:6

• ሙሴ የሰማንያ ዓመት ሰው ነበር፥ አሮንም የሰማኒያ ሦስት ዓመት ሰው ነበር (የተተወ ሀሳብና ቁጥሮችን የመተርጎም ዘዴ ተመልከት)

ለሙሴ ዕድሜው ሰማንያ ዓመት ሲሆን የአሮን ዕድሜው ሰማንያ ሦስት ዓመት ነበር።

Exodus 7:8

• ፈርዖን፦ ተአምራትን አሳዩኝ ሲላችሁ፥ አሮንን፦ በትርህን ወስደህ እባብ እንድትሆን በፈርዖን ፊት ጣላት በለው።

ፈርዖን እስቲ ተአምራት በማድረግ ማንነታችሁን ግለጡልኝ’ ቢላችሁ ለአሮን ንገረውና በትሩን ወስዶ በንጉሡ ፊት ይጣለው፤ በዚያን ጊዜ በትሩ ተለውጦ እባብ ይሆናል። (ቀጥተኛ እና ተዘዋዋሪ ንግግር ዕይነቶችን የመተርጎም ዘዴ ተመልከት)

Exodus 7:11

• የአሮን በትር ግን በትራቸውን ዋጠች

ነገር ግን የአሮን በትር የእነርሱን በትሮች ሁሉ ዋጠች።

• የፈርዖን ልብ ጸና (ምትካዊ ዘይቤ ተመልከት)

ፈርዖን ድፍረት አገኘ ማለት ሳይሆን ፈርዖን እምቢ አለ ወይም እልከኛ ማለት ነው።

Exodus 7:14

• የፈርዖን ልብ ደነደነ

ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም፥ እምቢተኛ ሆነ ማለት ነው

• እነሆ ወደ ውኃ ይወጣል (ግልጽ ያለሆነ ሀሳብ/ግምታዊ ዕውቀት/ ተመልከት)

ወደ አባይ (ናይል) ወንዝ በሚወርድበት/በሚሄድበት ጊዜ

Exodus 7:16

• እንዲህም ትለዋለህ

ለፈርዖን እንዲህ ብለህ ትነግረዋለህ

• እነሆ እኔ የወንዙን ውኃ በእጄ ባለችው በትር እመታለሁ

እነሆ፥ እኔ በዚህ በትር የአባይን ወንዝ ውሃ እመታለሁ

Exodus 7:19

• በግብፅም አገር ሁሉ

በግብፅ ምድር ደም በየቦታው ይሆናል

Exodus 7:20

• የፈርዖን ልብ ጸና (ምትካዊ ዘይቤ ተመልከት)

ፈርዖን ድፍረት አገኘ ማለት ሳይሆን ፈርዖን እምቢ አለ ማለት ነው።

• በወንዙ የነበሩ ዓሶች

ግልጽ ለማድረግ ከተፈለገ “በአባይ ወንዝ ውስጥ የነበሩ ዓሶች”

Exodus 7:23

• ግብፃውያንም ሁሉ

ብዙ ግብጻውያን ወይም የግብጽ ሰዎች ሁሉ


Chapter 8

1 ከዚያም እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ «ወደ ፈርዖን ሂድና እንዲህ በለው፤ ‹እግዚአብሔር የሚለው ይህ ነው፤ «እንዲያመልኩኝ ሕዝቤን ልቀቅ፡፡ 2 ካልህ፣ አገርህን በሙሉ በጓጕንቸው መቅሠፍት እመታዋለሁ፡፡ 3 ጓጕንቸር ይርመሰመሳል፡፡ ጓጕንቸሮቹ ከወንዙ ይወጡና ወደ ቤትህ፣ ወደ መኝታ ክፍልህና ወደ ዐልጋህ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ወደ አገልጋዮችህም ቤቶች ውስጥ ይገባሉ፡፡ ወደ ሕዝብህ፣ ወደ ምድጆችህና ወደ ቡሃቆችም ይዛመታሉ፡፡ 4 ጓጕንቸሮቹ አንተን፣ ሕዝብህንና አገልጋዮችህን ሁሉ ይመታሉ፡፡» 5 ለሙሴ እንዲህ አለ፤ «አሮንን፣ እጅህንና በትርህን በወንዞች፣ በምንጮችና በቦዮች ላይ ዘርጋና በግብፅ ምድር ላይ ጓጕንቸሮች እንዲወጡ አድርግ» በለው፡፡ 6 በግብፅ ውሆች ላይ እጁን ዘረጋ፤ ጓጕንቸዎቹም ወጥተው የግብፅን ምድር ሸፈኑት፡፡ 7 ጠንቋዮቹም በምትሃቸው ያንኑ አደረጉ፤ ጓጕንቸሮቹ በግብፅ ምድር ላይ እንዲወጡ አደረጉ፡፡ 8 ሙሴንና አሮንን አስጠርቶ፣ «ጓጕንቸሮቹን ከእኔና ከሕዝቤ ላይ አንዲያስወግድ ወደ እግዚአብሔር ጸልዩ፡፡ ከዚያም ለእግዚአብሔር እንዲሠዉ ሕዝቡን እለቃቸዋለሁ» አላቸው፡፡ 9 ፈርዖንን እንዲህ አለው፤ «ጓጕንቸሮቹ ከአንተና ከቤቶችህ እንዲወገዱ፣ በወንዙ ውስጥ ብቻ ግን እንዲቈዩ፣ ለአንተ፣ ለአገልጋዮችህና ለሕዝብህ የምጸልይበትን ጊዜ ለእኔ መንገሩ የአንተ ድርሻ ነው፡፡» 10 «ነገ» አለው፡፡ ሙሴም ፈርዖንን መልሶ፣ «እንደ አምላካችን እንደ እግዚአብሔር ያለ ማንም እንደሌለ እንድታውቅ አንተ እንደምትለው ይሁን፡፡ 11 ጓጕንቸሮቹ ከአንተ፣ ከቤቶችህ ከአገልጋዮችህና ከሕዝብህ ይወገዳሉ፡፡ በወንዙ ውስጥ ብቻ ግን ይቈያሉ» አለው፡፡ 12 አሮን ከፈርዖን ወጥተው ሄዱ፡፡ ሙሴም እግዚአብሔር በፈርዖን ላይ ስላመጣቸው ጓጕንቸሮች ወደ እግዚአብሔር ጮኸ፡፡ 13 ሙሴ እንደ ለመነው አደረገ፡- ጓጕንቸሮቹ በየቤቱ፣ በየግቢውና በየሜዳው ሞቱ፡፡ 14 ሕዝቡ የሞቱትን ሰብስበው ከመሯቸው፤ ምድሩም ከረፋ፡፡ 15 ነገር ግን ፈርዖን ፋታ መገኘቱን ሲያይ፣ ልቡን አደነደነ፤ እንደዚህ ያደርጋል ብሎ እግዚአብሔር ተናግሮ እንድ ነበረ፣ ሙሴንና አሮንንም አልሰማቸውም፡፡ 16 ለሙሴ እንዲህ አለ፤ «አሮንን እንዲህ በለው ‹በመላው የግብፅ ምድር ተባይ እንዲሆን የምድሩን ትቢያ በበትርህ ምታ፡፡» 17 እነርሱም እንዲሁ አደረጉ፡- አሮን እጁን ዘርግቶ በበትሩ የምድሩን ትቢያ መታው፡፡ በሰውና በእንስሳ ላይ ተባይ መጣ፡፡ የምድሩ ትቢያ ሁሉ በመላው የግብፅ ምድር ተባይ ሆነ፡፡ 18 በምትሃቸው ተባይ እንዲመጣ ሙከራ አደረጉ፤ ነገር ግን አልቻም፡፡ በሰውና በእንስሳ ላይ ተባዮች ነበሩ፡፡ 19 ጠንቋዮቹ ታዲያ ፈርዖንን፣ «ይህ የእግዚአብሔር ጣት ነው» አሉት፡፡ ነገር ግን የፈርዖን ልብ ደነደነ፤ እነርሱንም ለማድመጥ እምቢ አለ፡፡ ይህም የሆነው ፈርዖን እንዲህ እንደሚያደርግ እግዚአብሔር ተናግሮት በነበረው መሠረት ነው፡፡ 20 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ «በማለዳ ተነሣና ፈርዖን ወደ ወንዙ ሲወጣ በፊት ለፊቱ ቁም፡፡ እንደዚህም ብለህ ንገረው፤ ‹እግዚአብሔር የሚለው ይህ ነው፡- «እንዲያመልኩኝ ሕዝቤን ልቀቅ፡፡ 21 የማትለቅ ከሆነ ግን፣ በአንተ፣ በአገልጋዮችህና በሕዝብህ ላይ፣ ወደ ቤቶችህም ውስጥ የዝንብ መንጋ እልካለሁ፡፡ የግብፃውያን ቤቶች በዝንብ መንጋ ይሞላሉ፤ የሚቆሙበት ምድርም እንኳ ዝንብ ብቻ ይሆናል፡፡ 22 ግን በዚያ ቀን የዝንብ መንጋ እንዳይገኝባ፣ ሕዝቤ የሚኖርባትን የጌሤምን ምድር በተለየ ሁኔታ እይዛታለሁ፡፡ እኔ እግዚአብሔር በዚህ ምድር እንዳለሁ እንድታውቅ ይህ ይሆናል፡፡ 23 በሕዝቤና በሕዝብህ መካከል ልዩነት እንዲኖር አደርጋለሁ፡፡ ይህ ተአምራዊ ምልክት ነገ ነው የሚሆነው፡፡» 24 እግዚአብሔር እንዲሁ አደረገ፤ ጥቅጥቅ ያለ የዝንብ መንጋም ወደ ፈርዖን ቤትና ወደ አገልጋዮቹ ቤቶች መጣ፡፡ በመላው የግብፅ ውስጥ ምድሩ ከዝንቡ መንጋ የተነሣ ተበላሽቶ ነበር፡፡ 25 ሙሴንና አሮንን አስጠርቶ፣ «ሂዱና በምድራችሁ ለአምላካችሁ ሠዉ» አላቸው፡፡ 26 እንዲህ ለማድረግ ለእኛ ትክክል አይደለም፤ ለአምላካችን በእግዚአብሔር የምንሠዋቸው መሥዋዕቶች ለግብፃውያን አስጸያፊዎች ናቸውና፡፡ ለግብፃውያን አስጸያፊ የሆኑትን መሥዋዕቶች እያን በፊታቸው ብንሠዋ፣ በድንጋይ አይወግሩንም? 27 ባዘዘን መሠረት፣ ለአምላካችን ለእግዚአብሔር መሠዋት ያለብን ወደ ምድረ በዳወ የሦስት ቀን ጕዞ ሄደን ነው» አለ፡፡ 28 «እንድትሄዱና በምድረ በዳው ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር እንድትሠዉ እፈቅድላችኋለሁ፡፡ ርቃችሁ መሄድ ግን የለባችሁም፡፡ ለእኔም ጸልዩልኝ» አለ፡፡ 29 «ከአንተ ወጥቼ እንደ ሄድሁ፣ የዝንቦቹ መንጋ አንተን ፈርዖንን፣ አገልጋዮችህንና ሕዝብህን ነገ ለቀው እንዲሄዱ ወደ እግዚአብሔር እጸልይልሃለሁ፡፡ ነገር ግን ለእግዚአብሔር ለመሠዋት ሕዝባችን እንዲሄድ ባለመፍቀድ ከእንግዲህ ወዲያ ልታታልለን አይገባም» አለ፡፡ 30 ከፈርዖን ወጥቶ ሄደና ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ 31 እግዚአብሔር ሙሴ እንደ ለመነው አደረገ፡- የዝንቡን መንጋ ከፈርዖን፣ ከአገልጋዮቹና ከሕዝቡ ላይ አስወገደ፡፡ አንድም አልቀረም፡፡ 32 ነገር ግን ፈርዖን በዚህም ጊዜ ልቡ አደነደነ፤ ሕዝቡም እንዲሄድ አልፈቀደም፡፡



Exodus 8:1

• ወንዙም ጓጕንቸሮችን ያፈላል

የአባይ ወንዝ በጓጉንቸሮች በእንቁራርቶች የተሞላ ይሆናል ወይም በአባይ ወንዝ እንቁራርቶች ይሞላሉ

• በውኃ ማከማቻዎቹም

የዚህ ሀረግ ትርጉም ሁለት ነው። 1) በኲሬዎች ሁሉ ላይ 2) የጓጉንቸሮች መራቢያ ሥፍራዎች ሁሉ

Exodus 8:5

• አሮንን፦ በትርህን ይዘህ በወንዞቹና በመስኖቹ በውኃ ማከማቻዎቹም ላይ እጅህን ዘርጋ

በወንዞች፥ በቦይ ውሃዎችና በኩሬ ውሃዎች ላይ በእጁ ያለውን በትር እንዲያነሳ ለአሮን ንገረው

• የግብፅንም አገር ሸፈኑ

እንቁራርቶች ወጥተው የግብጽን ምድር ሞሉ ወይም ምድሪቱን አለበሱአት

Exodus 8:8

• ፈርዖንም ሙሴንና አሮንን ጠርቶ

ፈርዖንም ሙሴንና አሮንን አስጠርቶ ወይም ሙሴና ፈርዖን እንዲመጡ አድርጎ

• ለአንተ ለባሪያዎችህም ለሕዝብህም መቼ እንድጸልይ አስታውቀኝ

ለሹማምቶችህና ለሕዝብህ የምንፀልይበትን ጊዜ አንተው ወስን ወይም ለአንተና ለመኳንንትህና ለሕዝብህ የምጸልይበትን ሰዓት ብቻ ወስንልኝ ወይም ንገረን።

Exodus 8:10

• አምላካችንን እግዚአብሔርን የሚመስል እንደሌለ ታውቅ ዘንድ

አንተም እንደ አምላካችን እንደ እግዚአብሔር ያለ ሌላ አምላክ እንደሌለ እንዲታውቅ

• እንደ ቃልህ ይሁን

እንዳልከው አደርጋለሁ ወይም እንደ ነገርከኝ እፈጽማለሁ

• ከአንተ ከቤቶችህም ከባርያዎችህም ከሕዝብህም ይሄዳሉ

ሙሴ እያንዳንዱ ሰውና ሥፍራ በእንቁራርቶች እንደ ተወረረ እና ጭንቅ ውስጥ እንደገባ በመግለጽ መቅሰፍቱ እንደሚቆም አጽንኦት ሰጥቶ ይናገራል። በሌላ አገላለጽ፦ ከአንተ፥ ከቤትህ፥ ከሹማምንትህና ከሕዝብህ ሁሉ ዘንድ እንቁራርቶች ይወገዳሉ

Exodus 8:13

• ፈርዖንም ጸጥታ እንደሆነ ባየ ጊዜ ልቡን አደነደነ

ፈርዖን ችግሩ ካለፈና መረጋጋት ከሆን በኋላ እምቢ አለ።

• እግዚአብሔርም እንደተናገረ አልሰማቸውም

እግዚአብሔር (ያህዌ) እንዳለው ፈርዖን ሙሴንና አሮንን አልሰማቸው።

Exodus 8:16

• የምድሩን ትቢያ

የምድሩን ትቢያ ወይም አቧራ ወይም አፈር

• በግብፅ አገር ሁሉ የምድር ትቢያ ሁሉ ቅማል ሆነ

“ቅማል” የሚለው አንዳንደ ትንኝ ተብሎ ተተርጉሟል። በአማራጭነት ሁለቱንም ትርጉሞች መጠቀም ይቻላል። አማራጭ ትርጉም፦ በግብጽ አገር ያለውም ትቢያ ወይም አፈር ወይም አቧራ ሁሉ ወደ ተናካሽ ትንኝነት ወይም ወደ ቅማልነት ተለወጠ

Exodus 8:18

• የእግዚአብሔር ጣት ነው (ወካይ ዘይቤ)

“የእግዚአብሔር ጣት” የእግዚአብሔርን ሀይል ይወክላል። አማራጭ ትርጉም፦ “ይህ የእግዚአብሔር ሥራ ነው”

• የፈርዖን ልብ ግን ጸና (ምትካዊ ዘይቤ ተመልከት)

ፈርዖን ድፍረት አገኘ ማለት ሳይሆን ፈርዖን እምቢ አለ ማለት ነው።

Exodus 8:20

• በፈርዖንም ፊት ቁም

ንጉሱን ፈርዖንን አግኘው/በፊቱ ቅረብ

• ሕዝቤን ልቀቅ

ህዝቤ እንዲሄዱ ፈቃድ ስጣቸው

Exodus 8:22

አጠቃላይ ምልከታ፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል ለፈርዖን መናገሩን ቀጥሏል • በግብፅም አገር ሁሉ ላይ ከዝንቡ መንጋ የተነሣ ምድር ጠፋች

በተደራጊ ግስ የተጻፈው በአድራጊ ግስ ሲጻፍ፦ የዝንብ መንጋ የግብጽን ምድር ሁሉ ጎዳው።

Exodus 8:25

• በፊታቸው ብንሠዋ አይወግሩንምን?

በዕብራይስጡ “በዓይናቸው ፊት ብንሰዋ አይወግሩንም” ይላል። ይህ የተለመደ የዕብራውያንን አባባል ነው። ትርጉሙም አንድ ሰው በሚገኝበት ቦታ ወይም እርሱ ባለበት ሥፍራ እንደማለት ነው። አማርኛው በፊታቸው የሚለው የተፈጥሮ ፊታቸው ላይ ማለት ሳይሆን “እነርሱ ባሉበት ሥፍራ” ማለት ነው።

Exodus 8:28

• ነገር ግን ለእግዚአብሔር ይሠዋ ዘንድ ሕዝቡን እንዳይለቅቅ ፈርዖን እንደገና አያታልለን

ይህን ዐረፍተ ነገር በአዎንታዊ ሲንተረጉም፤ “ከእንግዲህ በኋላ አንተ እውነት ልትነግረንና ህዝባችንንም እንዲሄዱ መፍቀድ አለብህ”

• ፈርዖን እንደገና አያታልለን

ፈርዖን አንተ እንዲህ መናገር የለብህም ወይም ፈርዖን አንተ አታታልለን

Exodus 8:30

• ፈርዖንም . . . ልቡን አደነደነ

በዚህ ሀረግ አባባል ልቡን ያደነደነው እግዚአብሔር ሳይሆን ፈርዖን ራሱ አመጸኛ ሆነ፥ አልሰማም አለ። (ዘጸአት 7፡13 ተመልከት)


Chapter 9

1 ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ለሙሴ እንዲህ አለ፤ «ወደ ፈርዖን ሂድና እንዲህ ብለህ ንገረው፤ ‹የዕብራውያን አምላክ እግዚአብሔር ይህን ይናገራል፡፡ «እንዲያመልኩኝ ሕዝቤን ልቀቅ፡፡» 2 ብትልና አሁንም ከልክለህ ብታስቀራቸው፣ 3 የእግዚአብሔር እጅ መስክ ላይ ባለው ከብትህ፣ በፈረሶችህ፣ በአህዮችህ፣ በግመሎችህ፣ በፍየሎችህና በበጎችህ ላይ ይሆናል፤ አስከፊ በሽታም ያመጣል፡፡ 4 እግዚአብሔር በእስራኤል ከብትና በግብፅ ከብት መካከል ልዩነት አድርጓል፡- የእስራኤል ከብት አይሞትም፡፡ 5 ጊዜ ወስኖአል፤ «በምድሪቱ ላይ ይህን የማደርገው ነገ ነው» ብሎአል፡፡ 6 ይህን በሚቀጥለው ቀን አደረገው፡- የግብፅ ከብት ሁሉ ሞተ፡፡ ከእስራኤል ከብት ግን አንድም አልሞተም፡፡ 7 ተከታትሎ አጣራ፣ ከእስራኤል ከብት አንድም እንኳ አለመሞቱን ተረዳ፡፡ ነገር ግን ልቡ ደንድኖ ነበር፤ ስለዚህ ሕዝቡ እንዲሄድ አልፈቀደም፡፡ 8 እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን አላቸው፤ «ከምድጃ ላይ እፍኝ ዐመድ ውሰዱና አንተ ሙሴ ወደ ሰማይ ፈርዖን እያየ ዐመዱን በትነው፡፡ 9 በግብፅ ምድር ሁሉ ላይ ትቢያ ይሆናል፡፡ ይህም በመላው የግብፅ ምድር በሰውና በእንስሳት ላይ ዕባጭና ቊስል ያመጣል፡፡» 10 ስለዚህ ሙሴና አሮን ከምድጃ ዐመድ ወስደው ከፈርዖን ፊት ለፊት ቆሙ፡፡ ከዚያም ሙሴ ዐመዱን ወደ ሰማይ በተነው፡፡ ዐመዱ በሰውና በእንስሳ ላይ የሚወጣ ዕባጭና ቊስልን አመጣ፡፡ 11 በእነርሱና በሌች ግብፃውያን ሁሉ ላይ ወጥቶ በነበረው ዕባጭ ምክንያት ጠንቋዮቹ በሙሴ ፊት መቆም አልቻሉም፡፡ 12 እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ ስለ አደነደነው፣ ፈርዖን ሙሴንና አሮንን አልሰማቸውም፡፡ ይህም የሆነው ፈርዖን እንደዚህ እንደሚደርግ እግዚአብሔር ለሙሴ ነግሮት እንድ ነበረው ነው፡፡ 13 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ «በጠዋት ተነሣና ከፈርዖን ፊት ለፊት ቁም፤ እንደዚህ ብለህም ንገረው፤ ‹የዕብራውያን አምላክ እግዚአብሔር ይህን ተናገሯል፡- «እንዲያመልኩኝ ሕዝቤን ልቀቅ፡፡ 14 ጊዜ በአንተ በራስህ፣ በአገልጋዮችህና በሕዝብህ ላይ መቅሠፍቴን ሁሉ እልካለሁ፡፡ ይህን የማየደርገውም በድምር ሁሉ እንደ እኔ ያለ እንደሌለ እንድታውቅ ነው፡፡ 15 ጊዜ እጄን ዘርግቼ አንተንና ሕዝብህን በበሽታ በመምታት ከምድር ባጠፋኋችሁ ነበር፡፡ 16 ግን በሕይወት እንድትቈይ ያደረግሁህ፣ ኀይሌን እንድገልጥብህና ስሜም በምድር ሁሉ እንዲታወቅ ነው፡፡ 17 ሕዝቤን እንዳይሄድ በማድረግ በሕዝቤ ላይ ራስህን እያሳበይህ ነው፡፡ 18 ነገ በዚህ ጊዜ ከተመሠረተችበት ቀን ጀምሮ እስካሁን ድረስ በግብፅ ታይቶ የማይታወቅ ከባድ የበረዶ ማዕበል አመጣለሁ፡፡ 19 አሁን ሰው ላክና ከብትህን፣ በመስክ ላይ ያለህን ማንኛውንም ነገር ወደ ጠለያ ስፍራ ሰብስብ፡፡ መስክ ላይ የቀረና ወደ ቤት ያልመጣ ማንኛውም ከብትና ሰው ሁሉ በረዶው ይወርድባቸውና ይሞታሉ፡፡» 20 አገልጋዮች የእግዚአብሔር ቃል የተቀበሉት ባሮቻቸውንና ከብቶቻቸውን ወደ ቤት ለማምጣት ተጣደፉ፡፡ 21 የእግዚአብሔርን ቃል ከምር ያልተቀበሉት ግን ባሮቻቸውንና ከብታቸውን መስክ ላይ ተዉ፡፡ 22 ሙሴን እንዲህ አለው፤ «በሁሉም የግብፅ ምድር፣ በሕዝብ፣ በእንስሳትና በመላው የግብፅ ምድር መስክ ላይ ባሉ ተክሎች ሁሉ ላይ በረዶ እንዲወርድ እጅህን ወደ ሰማይ ዘርጋ፡፡» 23 በትሩን ወደ ሰማይ ዘረጋ፤ እግዚአብሔርም ነጐድጓድ፣ በረዶና መብረቅ ወደ ምድር ላከ፡፡በግብፅም ምድር ላይ በረዶ አዘነበ፡፡ 24 ግብፅ አገር ከሆነችበት ጊዜ ጀምሮ በምድሪቱ ሁሉ ያልታየ እጅግ ከባድ የበረዶና የመብረቅ ቅልቅል ነበር የዘነበው፡፡ 25 የግብፅ ምድር፣ በረዶው መስክ ላይ ያለውን ማንኛውንም ነገር፣ ሰውንም እንስሳቱንም መታ፡፡ በመስክ ያለውን ተክል ሁሉ መታው፣ ዛፉንም ሁሉ ሰባበረው፡፡ 26 እስራኤላውያን በሚኖሩበት በጌሤም ምድር ብቻ በረዶ አልነበረም፡፡ 27 በኋላ ፈርዖን ሙሴንና አሮንን እንዲጠሩ ሰዎችን ላከ፡፡ እንዲህም አላቸው፤ «በዚህ ጊዜ ኀጢአት ፈጽሜአለሁ፡፡ እግዚአብሔር ጻድቅ ነው፤ እኔና ሕዝቤ ግን ኀጢአተኞች ነን፡፡ 28 እግዚአብሔር ጸልዩ፤ ምክንያቱም ከባዱ ነጐድጓድና በረዶ እጅግ በዝቶብናል፡፡ እለቅቃችኋለሁ፤ ከእንግዲህ ወዲያ እዚህ አትቆዩም፡፡ 29 ፈርዖንን እንዲህ አለው፤ «ከከተማዪቱ እንደ ወጣሁ፣ እጆቼን ወደ እግዚአብሔር እዘረጋለሁ፡፡ ነጐድጓዱ ያቆማል፣ በረዶም አይኖርም፡፡ በዚህ መንገድ አንተ ምድር የእግዚአብሔር መሆኗን ታውቃለህ፡፡ 30 ግን አንተንና አገልጋዮችህን በሚመለከት እግዚአብሔር አምላክን ገና በእውነት እንደማታከብሩ ዐውቃለሁ፡፡» 31 ጊዜ ተልባው አብቦ፣ ገብሱም ፍሬ በመያዝ ላይ ነበረ፣ ተልባውና ገብሱ ከጥቅም ውጭ ሆነዋል፡፡ 32 አጃው ግን ቈይተው የሚደርሱ ሰብሎች በመሆናቸው አልተጐዱም፡፡ 33 ሙሴ ከፈርዖንና ከከተማዪቱ ሲወጣ፣ እጆቹን ወደ እግዚአብሔር ዘረጋ፤ ነጐድጓዱና በረዶው ቆሙ፤ ዝናብም አልዘነበም፡፡ 34 ፈርዖን ዝናቡ፣ በረዶውና ነጐድጓዱ መቆሙን ሲያይ፣ እንደ ገና ኀጢአት አደረገ፤ ከአገልጋዮቹ ጋርም በአንድነት ልቡን አደነደነ፡፡ 35 የፈርዖን ልብ ስለ ደነደነ፣ የእስራኤል ሕዝብ እንዲሄዱ አልፈቀደም፡፡ ይህም የሆነው ፈርዖን ልቡን እንድሚያደነድን እግዚአብሔር ለሙሴ ነግሮት የነበረው መንገድ ነው፡፡



Exodus 9:1

ጠቅላላ ምልከታ፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) ከሙሴ ጋር መነጋገሩንና ፈርዖን የእስራኤልን ህዝብ ከግብጽ ምድር አውጥቶ እንድለቃቸው የተለያዩ ምልክቶችን ሲያደርግ እንመለከታለን። • ልትለቅቃቸውም እንቢ ብትል ብትይዛቸውም

“ልትለቅቃቸውም እንቢ ብትል ብትይዛቸውም” ሁለቱም አባባሎች ተመሳሳይ ናቸው። ፈርዖን ህዝቡን ለመልቀቅ እምቢ ብል ልደርስበት ያለውን ነገር ለማሳየትና ትኩረት ለመስጠት ሲፈለግ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እስራኤላውያንን ለመልቀቅ ባትፈልግና እምቢ ብትል

• እነሆ የእግዚአብሔር እጅ በሜዳ ውስጥ ባሉት ከብቶች ላይ ይሆናል

“የእግዚአብሔር እጅ” የሚለው ሀረግ እግዚአብሔር ከብቶችን በበሽታ ለመጉዳት ሀይል እንዳለው የሚያመለክት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “የእግዚአብሔር (ያህዌ) ሀይል ከብቶችህን ይቀስፋል ወይም ይገድላል”

• በከብቶችህ

በፈርዖን ከብቶች ላይ የሚመጣ መቅሰፍት መሆኑን ያሳያል፤ ነገር ግን ፈርዖን የግብጽን ህዝብ ሁሉ በመወከል የቀረበ አነጋገር ነው።

• በእስራኤል ከብቶች

“በእስራኤል ከብቶች” የተባለው የእስራኤላውያንን ከብቶች የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የእስራኤላውያን የሆኑ ከብቶች

• በግብጽ ከብቶች

“በግብጽ ከብቶች” የተባለው የግብጻውያንን ከብቶች የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የግብጻውያን የሆኑ ከብቶች

Exodus 9:5

• ጊዜን ወሰነ

ጊዜ ቀጠረ ወይም ጊዜ ለየ ወይም ጊዜ ወሰነ

• የግብፅም ከብት ሁሉ ሞተ

ይህ ግነታዊ ዘይቤ ዓይነት ነው። በርግጥ በዚህን ጊዜ የግብጻውያን ከብቶች ሁሉ አልሞቱም፤ ምክንያቱም በኋለኛው መቅሰፍት የሞቱ ሌሎች ከብቶች አሉ። በትርጉም ሥራ ወቅት “ሁሉ” የሚለው ቃል መቅረት የለበትም።

• የግብጽም ከብት ሁሉ

“ግብጽ” የሚለው ምድሪቱን ለማመልከት ሳይሆን የግብጽ ሰዎችንና ከብቶቻቸው ማለት ነው።

• ፈርዖንም ላከ

ንጉሡ የሆነውን ሁሉ ለማጣራት ሰዎችን በላከ ጊዜ ወይም ፈርዖን ያጣሩ ዘንድ ሰዎች ልኮ

• እነሆም

ይህ ቃል የሚያመለክተው ፈርዖን በሆነው ነገር እጅግ መገረሙን የሚያሳይ ነው።

• የፈርዖን ልብ ግን ደነደነ

በዚህኛ ክፍል “ፈርዖን ልቡን አደነደነ” ወይም “እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ አጸና” ሳይሆን “የፈርዖን ልብ ግን ደነደነ” የሚለው ትኩረቱ ልቡ እንደ ሰው ለመታዘዝ ፈቃደኛ አልሆነም ማለት ነው።

Exodus 9:8

• ከምድጃ አመድ ውሰዱ

እሳት ከሚነድበት ቦታ እፍኝ ዐመድ ውሰዱ

• ሻህኝ የሚያወጣ ቍስል ሆነ

መግል የሚቋጥር ቁስል ወይም ቡጉንጅ ወይም እባጭ ዓይነት ቁስል ሆነ ማለት ነው

Exodus 9:11

• እግዚአብሔርም የፈርዖንን ልብ አጸና (ዘጸአት 7፡13)

የፈርዖን ልብ የተባለው ራሱ ፈርዖን ማለት ነው። ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም ወይም እምብ አለ ማለት ነው። (ወካይ ወይም ተለዋጭ ዘይቤ ተመልከት)። በዚህኛ ክፍል የፈርዖንን ልብ ያደነደነው ወይም ፈርዖን እንዳይሰማ ያደረገው እግዚአብሔር እንደሆነ ይገልጻል።

Exodus 9:13

• በሰውነትህ

በአንተ ላይ ወይም አንተን ራስህን መቅሰፍቱ ይጎዳሃል ማለት ነው።

Exodus 9:15

• እጄን ዘርግቼ

እግዚአብሔር በታላቅ ሀይሉ ለማጥቃት ወይም ለመጉዳት ሲነሳ ማለት ነው። “እኔ እጄን ዘርግቼ” ሲል ሀይሌን ለመግለጥ ሲነሳ ወይም ሀይሌን ሲገልጥ ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “አንተን ለመቅጣት ሀይሌን ሲጠቀም”

• ስሜም በምድር ሁሉ ላይ ይነገር ዘንድ

“ስሜ” የሚለው የእግዚአብሔር (ያህዌ) ዝና የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ ትልቅ እንደሆንኩ ሰዎች እስኪያውቁ ድረስ

• ስለዚህ አስነሥቼሃለሁ

ፈርዖን እስራኤላውያን እንዳይሄዱ ሲያደርግና እንቅፋት ሲሆንባቸው ምክንያቱ እግዚአብሔር ያንን እንዲያደርግ ስለፈቀደ ነው።

Exodus 9:18

• ከተመሰረተች ጀምሮ

በሌላ አገላለጽ፦ ግብጽ እንደ አገር ከታወቀችበት ወይም ከተቋቋመች ጊዜ ጀምሮ ማለት ነው

• አሁን እንግዲህ ላክ፥ ከብቶችህንም በሜዳም ያለህን ሁሉ አስቸኵል

በመስክ የተሰማሩ ከብቶችህና ከቤት ውጪ ያለ ማንኛውንም የአንተ ንብረት ሁሉ በፍጥነት ወደ መጠለያ እንዲያስገቡ ለአገልጋዮችህ አሁን ትእዛዝ ስጥ።

Exodus 9:20

• ከፈርዖንም ባሪያዎች የእግዚአብሔርን ቃል የፈራ

እግዚአብሔር (ያህዌ) ስለተናገረው ነገር የፈሩት የፈርዖን ሹማምት ወይም እግዚአብሔር የተናገረውን ነገር ሰምተው የታዘዙት የፈርዖን ሹማምት

• የእግዚአብሔርንም ቃል ያላሰበ

እግዚአብሔር የተናገረውን ቃል ያልታዘዘ ወይም ችላ ያለ ወይም ለመስማት ፈቃደኛ ያልሆነ

Exodus 9:22

• እጅህን ወደ ሰማይ ዘርጋ

x

Exodus 9:25

• ሰውንና እንስሳን መታ

ሕዝቡንና ከብቶችን ጭምር ገደለ ወይም በህዝብና በከብቶች ላይ አደጋ አደረሰ

• የእስራኤል ልጆች ተቀምጠው በነበሩባት

እስራኤላውያን ወይም የእስራኤል ህዝብ በሚኖሩባት

Exodus 9:27

• እጄን ወደ እግዚአብሔር እዘረጋለሁ

እጅን ወደ ላይ ማንሳት በሌላ መልኩ ለጸሎት መዘርጋት የሚያመለክት ተምሳሌት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “እጄን ዘርግቼ ወደ እግዚአብሔር እጸልያለሁ”

• አምላክን እግዚአብሔርን ገና እንደማትፈሩ

ለእግዚአብሔር ክብር እንደምትሰጡ፥ እግዚአብሔርን እንደማትታዘዙ

Exodus 9:31

• ተልባ

የእህል ዓይነት በተለይ የጥራጥሬ ዓይነት ነው።

• ገብስ

የእህል ዓይነት ለሰዎችና ለከብቶች ምግብነት የሚውል

• አጃ

የስንዴና የገብስ ዘር የሆነ የእህል ዓይነት

• እጁንም ወደ እግዚአብሔር ዘረጋ

እጁን ወደ ላይ አንስቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ

Exodus 9:34

• ኃጢያትን ጨመረ

እንደገና ኃጢአት ሠራ


Chapter 10

1 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ «የፈርዖንና የአገልጋዮቹን ልብ አደነድናለሁና ወደ ፈርዖን ሂድ፡፡ እነዚህን የተአምራቴን ምልክቶች ለማሳየት ይህን አድርጌአለሁ፡፡ 2 ይህን ያደረግሁት ግብፃውያንን እንዴት በከባድ አያያዝ እንደያዝኋቸውና በመካከላቸውም የተአምራትን ልዩ ልዩ ምልክቶች እንዳሳየሁ ለልጆቻችሁና ለልጅ ልጆቻችሁ እንድትነግሯቸው ነው፡፡ በዚህ መንገድ እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ፡፡ 3 አሮንም ወደ ፈርዖን ሄደው እንዲህ አሉት፤ «የዕብራውያን አምላክ እግዚአብሔር የሚለው ይህ ነው፡- ‹ራስህን በፊቴ ለማዋረድ እምቢ የምትለው እስከ መቼ ነው? እንዲያመልኩኝ ሕዝቤን ልቀቅ፡፡ 4 ግን ሕዝቤን አልለቅም ብትል፣ እነሆ፣ በነገው ቀን በአገርህ ላይ አንበጣዎችን አመጣለሁ፡፡ 5 ማንም ሰው መድሩን ማየት እስከማይችል ድረስ የምድሩን ገጽ ይሸፍኑታል፡፡ ከበረዶው አምልጦ የቀረውን ሁሉ ይበሉታል፡፡ መስክ ላይ የሚያድግላችሁንም ዛፍ ሁሉ ይበሉታል፡፡ 6 አንበጣዎቹ የአንተን፣ የአገልጋዮችህን ቤቶች ሁሉ ይሞሏቸዋል፤ ይህም፣ አባትህም አያትህም በዚህ ምድር ላይ መኖር ከጀመሩበት ቀን አነሥቶ እስከዚህ ጊዜ ድረስ ታይቶ የማይታወቅ ነው፡፡» ሙሴም ከፈርዖን ዘንድ ወጥቶ ሄደ፡፡ 7 ፈርዖንን፣ «ይህ ሰው ወጥመድ የሚሆንብን እስከ መቼ ነው? አምላካቸውን እግዚአብሔርን እንዲያመልኩት እስራኤላውያን ይሂዱ፡፡ ግብፅ መጥፋቷን ገና አልተገነዘብህምን?» አሉት፡፡ 8 ሙሴና አሮን፣ «ሂዱ አምላካችሁን እግዚአብሔርን አምልኩ፡፡ ነገር ግን የሚሄዱት የትኞቹ ናቸው?» ወዳላቸው ወደ ፈርዖን እንደገና እንዲመጡ ተደረገ፡፡ 9 የምንሄደው ከወጣቶቻችንና ከሽማግሌዎቻችን፣ ከወንድና ከሴት ልጆችን ጋር ነው፡፡ ለእግዚአብሔር በዓል ማክበር ስለሚገባን፣ የበግና የፍየል መንጎቻችንን፣ የቀንድ ከብቶቻችንንም ይዘን እንሄዳለን» አለ፡፡ 10 ፈርዖንም እንዲህ አላቸው፤ «እናንተንና ታናናሽ ልጆቻችሁን ስለችሁ፣ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን፡፡ ነገር ግን ተመልከቱ፣ ክፉ ነገር ዐስባችኋል፡፡ 11 ከመካከላችሁ ወንዶች ብቻ ይሂዱና እግዚአብሔርን ያምልኩ፤ የምትፈልጉት ያንን ነውና፡፡» ከዚያም በኋላ ሙሴና አሮን ከፈርዖን ዘንድ እንዲወጡ ተደረገ፡፡ 12 እግዚአብሔርም ሙሴን፣ «አንበጣዎች የግብፅን ምድር እንዲወርሩትና ከበረዶው ተርፎ የቀረውን፣ በምድሩ ያለውን ተክል ሁሉ እንዲበሉት እጅህን በግብፅ ምድር ላይ ዘርጋ» አለው፡፡ 13 ሙሴም በትሩን በግብፅ ምድር ላይ ዘረጋ፤ እግዚአብሔርም በዚያ ቀንና ሌሊት ሁሉ የምሥራቅ ነፋስ በምድሩ ላይ እንዲነፍስ አደረገ። ማለዳ ላይ የምሥራቁ ነፋስ አንበጣዎቹን አምጥቶ ነበር። 14 በግብፅ ምድር ሁሉ ተሠራጩ፤ አገሩንም ሁሉ ወረሩት። እንደዚህ እጅግ የበዙ አንበጣዎች በምድሩ ውስጥ ከዚህ በፊት አልነበሩም፤ ወደፊትም አይኖሩም። 15 ጨለማ እስኪሆን ድረስ የምድሩን ሁሉ ገጽ ሸፈኑት። በምድሩ ላይ ያለውን ማንኛውንም ተክልና ከበረዶው ተርፎ የቀረውን የዛፍ ፍሬ ሁሉ በሉት። በግብፅ ምድር ሁሉ ለምለም ቅጠል ያለው ተክል አልቀረም፤ በመስክም ላይ ምንም ዛፍ አልነበረም። 16 ሙሴንና አሮንን በፍጥነት አስጠርቶ እንዲህ አላቸው፤ “በአምላካችሁ በእግዚአብሔርና በእናንተ ላይ ኀጢአት ሠርቻለሁ። 17 እንግዲህ አሁን ኀጢአቴን ይቅር በሉኝና ይህን ሞት ከእኔ እንዲያስወግድልኝ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ጸልዩልኝ።” 18 ስለዚህ ሙሴ ከፈርዖን ዘንድ ወጥቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። 19 አንበጣዎቹን ለቃቅሞ ወደ ቀይ ባሕር የሚከትታቸውን ብርቱ የምዕራብ ነፋስ አመጣ፤ በግብፅ ግዛት ሁሉ የቀረ አንድም አንበጣ አልነበረም። 20 ነገር ግን እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ ስላደነደነው፣ ፈርዖን እስራኤላውያንን አልለቀቃቸውም። 21 ሙሴን፣ “በግብፅ ምድር ላይ የሚዳስስ ከባድ ጨለማ እንዲሆን እጅህን ወደ ሰማይ ዘርጋ” አለው። 22 እጁን ወደ ሰማይ ዘረጋ፤ በግብፅም ምድር ሁሉ ለሦስት ቀን ድቅድቅ ጨለማ ሆነ። 23 ቀኖች አንዱ ሌላውን ማየት አልቻለም፤ ከቤቱም የወጣ ማንም የለም። ለእስራኤላውያን ግን በሚኖሩበት ስፍራ ብርሃን ነበራቸው። 24 ፈርዖን ሙሴን አስጠርቶ፣ “ሂዱ እግዚአብሔርን አምልኩ። ቤተ ሰቦቻችሁም እንኳ ዐብረዋችሁ መሄድ ይችላሉ፤ በጎቻችሁና ከብቶቻችሁ ግን እዚህ መቅረት አለባቸው” አለው። 25 እንዲህ አለው፤ “ለአምላካችን ለእግዚአብሔር እንድንሠዋቸው ለመሥዋዕትና ለሚቃጠል መሥዋዕት እንስሳቱንም ልትሰጠን ይገባል። 26 ከብቶቻችንም ከእኛ ጋር መሄድ አለባቸው፤ አምላካችንን እግዚአብሔርን ለማምለክ ልንወስዳቸው ይገባልና ከእነርሱ ሰኮናም እንኳ እዚህ አይቀርም። ምክንያቱም እግዚአብሔርን በምን እንደምናመልከው እዚያ እስክንደርስ ድረስ አናውቅም።” 27 ግን የፈርዖንን ልብ ስላደነደነው ፈርዖን ሕዝቡን አልለቀቃቸውም። 28 ሙሴን፣ “ሂድ ከእኔ ዘንድ! ፊቴን እንዳታይ ተጠንቀቅ፤ ፊቴን ባየህበት ቀን ትሞታለህና” አለው። 29 ሙሴም፣ “አንተ ራስህ ተናግረሃል። ፊትህን እንደ ገና አላየውም” አለው።



Exodus 10:1

• የእርሱን የባሪያዎቹንም ልብ አደንድኜአለሁና (ተለዋጭ ዘይቤ)

እግዚአብሔር ፈርዖንና ሹማምንቱን የማይሰሙና የማይታዘዙ መሆናቸውን ለመግለጽ ልባቸውን አደንድኛለሁ ይላል። (ዘጸአት 9፡12 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት)።

• ይህችንም ተአምራቴን

የዕብራይስጡ ቅጂ “እነዚህን ታአምራት” ይላል። አንድ ታአምር ሳይሆን ብዙ ታአምራትና ምልክቶችን አድርጓል ማለት ነው። አዲሱ መደበኛ አማርኛ ቅጂም እንደ ዕብራይስጡ “እነዚህን ታአምራት” ይላልና ተርጓሚዎች ትኩረት ሊሰጡት ይገባል።

Exodus 10:3

• እግዚአብሔር እንዲህ ይላል

ሙሴና አሮን የሚናገሩት ቃል የራሳቸው ሳይሆን የእግዚአብሔር መሆኑን ያሳያል። እነርሱም ተልከው የሄዱት በእግዚአብሔር ነውና።

Exodus 10:5

• በረዶ

ከዝናብ ጋር አብሮ የሚወርድ እህልና ቡቃያ የሚያጠፋ ነው

Exodus 10:7

• ዕንቅፋት ይሆንብናል

ዕንቅፋት መሆን ማለት ችግር ፈጣሪ፥ ፀብ ጫሪ ሰው እንደማለት ነው።

• ይህ ሰው እስከ መቼ ዕንቅፋት ይሆንብናል? (አጋናኝ ጥያቄ)

የፈርዖን ሹማምት ይህን ጥያቄ የጠየቁት በዚህ ሰው ምክንያት በግብጽ ምድር ጥፋት መምጣቱን ለማመልከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “ይህ ሰው በእኛ ላይ ጥፋት እንዲያመጣ አንፈቅድለትም”

• ግብፅስ እንደ ጠፋች ገና አታውቅምን?

የፈርዖን ሹማምት ንጉሱን ይህን ጥያቄ የጠየቁት ግብጽ በጥፋት ላይ መሆኗን ፈርዖን ማየት ወይም ማስተዋል ባለመቻሉ ነበር። አማራጭ ትርጉም፦ “ግብጽ በጥፋት ላይ መሆኗን አስተውል”። እነዚህ መቅሰፍቶች ግብጽን አጥፍተዋል ወይም “የሙሴና አሮን አምላክ ግብጽን አውድሟታል” እንደማለት ነው።

• ከፈርዖንም ፊት አባረሩአቸው

ፈርዖን ሙሴንና አሮንን ከፊቱ አባረራቸው ወይም ፈርዖን ሙሴንና አሮንን እንዲያባርሩዋቸው እንዲያስወጧቸው አገልጋዮቹን አዘዘ ማለት ነው

Exodus 10:9

• እናንተን ከልጆቻችሁ ጋር ስለቀቅ

ፈርዖን ይህን ያለው እስራኤላውያንና ልጆቻቸውን ለመልቀቅ እንደማይፈልግ ለማሳየት ነው።

• ከፈርዖንም ፊት አባረሩአቸው

ሙሴና አሮን ከፈርዖን ፊት እንዲወጡ ተደረገ ወይም ሙሴና አሮን የግድ ከፈርዖን ፊት እንዲወጡ አደረጓቸው

Exodus 10:12

• የምሥራቅን ነፋስ

“የምስራቅ ነፋስ” ማለት ከምስራቅ በኩል የሚነፍስ ነፋስ ወይም ከምስራቅ በኩል የሚነሳ ነፋስ ማለት ነው።

• በግብፅ አገር ላይ እንዲወጡ

አንበጦች በግብጽ ምድር ላይ እንዲመጡ ወይም አንበጦች የግብጽን ምድር እንዲወሩ እንደማለት ነው።

Exodus 10:14

• የምድሩንም ፊት ፈጽመው ሸፈኑት አገሪቱም ጨለመች

ከአንበጣው ብዛት የተነሳ አገሪቱ ጠቁራ ጨለማ እስክትመስል ድረስ የአንበጣ መንጋ ሸፈናት ማለት ነው።

Exodus 10:16

• አንድ ጊዜ ብቻ

በተጨማሪ ወይም አንድ ዕድል ስጡኝና እንደ ማለት ነው።

• ይህም ሞት ብቻ ከእኔ ያነሣልኝ ዘንድ

በዚህ ቦታ “ሞት” የተባለው በአንበጦች ምክንያት የመጣውን መቅሰፍት ወይም ጥፋት ለማመልከት ነው። ይህ ጥፋት እየከፋ ሲሄድ ሞት እንደሚያስከትል ለመግለጽም ጭምር ነው።

Exodus 10:19

• እግዚአብሔርም ከምዕራብ ዐውሎ ነፋሱን አስወገደ

የዚህ ዐረፍተ ነገር ትክክለኛ ትርጉም እግዚአብሔርም አንበጦቹንም ጠራርጎ ወደ ቀይ ባሕር የሚነዳ ብርቱ ነፋስ ከምዕራብ በኩል አስነሣ ወይም ያህዌ ነፋሱን ወደ ብርቱ የምዕራብ ነፋስ ለወጠው ያም ነፋስ አንበጣዎቹን እየነዳ ወደ ቀይ ባህር ከተታቸው ማለት ነው።

• እግዚአብሔርም የፈርዖንን ልብ አጸና

የፈርዖን ልብ የተባለው ራሱ ፈርዖን ማለት ነው። ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም ወይም እምቢ አለ ማለት ነው። (ዘጸአት 9፡12 ተመልከት)።

Exodus 10:21

• ፅኑ ጨለማ ይሁን

ድቅድቅ ጨለማ ወይም በእጅ እንደምዳሰስ ዓይነት ጨለማ

Exodus 10:24

• አንድ ሰኮናም አይቀርም (ወካይ ዘይቤ)

አንድ ሰኮናም የሚለው “ሙሉ ከብቱን” ለማመልከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ አንድ ከብት እንኳን አናስቀርም

Exodus 10:27

• እግዚአብሔርም የፈርዖንን ልብ አጸና

የፈርዖን ልብ የተባለው ራሱ ፈርዖን ማለት ነው። ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም ወይም እምብ አለ/እምብተኛ/ ሆነ ማለት ነው። ዘጸአት 9፡12 ተመልከት።

• ሊለቅቃቸው አልወደደም

በሌላ አገላለጽ፦ ፈርዖንም ሕዝቡን መልቀቅ አልፈለገም

• ፊቴን እንዳታይ ተጠንቀቅ (ወካይ ዘይቤ)

“ፊት” የሚለው “ሰውዬውን” ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔን እንዳታይ ተጠንቀቅ

• እንደ ተናገረህ ይሁን

በዚህ አባባል ሙሴ የፈርዖንን ንግግር ሲያጸናው እንመለከታለን። አንተ የተናገርከው እውነት ነው እንደማለት ነው። (ፈሊጣዊ ንግግር)


Chapter 11

1 ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ለሙሴ እንዲህ አለ፤ “በፈርዖንና በግብፅ ላይ የማመጣው ገና አንድ መቅሠፍት አለ። ከዚያ በኋላ ከዚህ እንድትሄዱ ይፈቅድላችኋል። በመጨረሻ እንድሄድ ሲያደርግም፣ ሙሉ በሙሉ ያባርራችኋል። 2 ወንድና እያንዳንዱ ሴት ከጎረቤቱ ወይም ከጎረቤቱ የብርና የወርቅ ዕቃዎችን ስጡን ብለው እንዲጠይቁ ለሕዝቡ ተናገር።” 3 እስራኤላውያንን ደስ ለማሰኘት ግብፃውያን እንዲነሣሡ አደረገ። ሙሴም በፈርዖን አገልጋዮችና በግብፅ ሕዝብ ዘንድ እጅግ የሚደነቅ ሰው ሆነ። 4 እንዲህ አለ፤ “እግዚአብሔር ይህን ተናግሯል፦ ‘እኩለ ሌሊት ላይ በመላው ግብፅ ዐልፋለሁ። 5 ላይ ከሚቀመጠው ከፈርዖን በኵር ልጅ ጀምሮ፣ ወፍጮ ላይ እስከምትፈጨዋ እስከ ባሪያዪቱ በኵር ልጅና እስከ እንስሳቱ በኵር ሁሉ ድረስ በግብፅ ምድር ያሉ በኵር በሙሉ ይሞታል። 6 በቀድሞው ጊዜ ያልነበረ እንደገናም የማይደገም ታላቅ ዋይታ በግብፅ ምድር ሁሉ ይሆናል። 7 ሕዝብ ላይ ግን፣ በሰውም ሆነ በእንስሳ ላይ ውሻ እንኳ አይጮኽም። በዚህም ግብፃውያንንና እስራኤላውያንን የማስተናግድበት መንገድ የተለያየ እንደ ሆነ ታውቃላችሁ።’ 8 እነዚህ አገልጋዮችህ ሁሉ ወደ እኔ ይመጣሉ፤ ለእኔም ይሰግዳሉ። ‘አንተና ተከታዮችህ ሁሉ ሂዱ!’ ብለውም ይናገራሉ። ከዚያ በኋላ እወጣለሁ።” ከዚያም ሙሉ ከፈርዖን ዘንድ በትልቅ ቊጣ ወጥቶ ሄደ። 9 ሙሴን፣ “ፈርዖን እናንተን አይሰማችሁም። ይህም የሆነው ብዙ አስደናቂ ነገሮችን በግብፅ ምድር ላይ እንዳደርግ ነው” አለው። 10 አሮን እነዚህን ድንቆች ሁሉ በፈርዖን ፊት አደረጉ። ነገር ግን እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ ስላደነደነው፣ ፈርዖን የእስራኤል ሕዝብ ከምድሩ እንዲወጡ አልፈቀደም።



Exodus 11:1

• ሲለቅቃችሁም አባርሮ ይሰድዳችኋል

አንድ ሰው እንዳይቀር ሁላችሁንም በማባረር ያስወጣችኋል

• በሕዝቡ ጆሮ ተናገር

ለህዝብ መናገርን በወካይ ዘይቤ ተጠቅሞ ለጆሮአቸው ተናገር ይላል። በሌላ አገላለጽ፦ ለህዝቡ ተናገር

• ሙሴም በፈርዖን ባሪያዎችና በሕዝቡ ፊት በግብፅ አገር እጅግ የከበረ ሰው ነበረ

የግብጽ ንጉስ ፈርዖን፤ ሹማምቱና ሕዝቡ ሁሉ ሙሴ ታላቅ ወይም የከበረ ሰው አድርገው ይቀበላሉ

Exodus 11:4

• በግብፅም አገር ያለ በኵር ሁሉ

በኩር የሚለው ቃል ሁል ጊዜ መጀመሪያ የተወለደን ወንድ (ሰውና እንስሳ) የሚመለከት ነው።

• በዙፋኑ ከሚቀመጠው

ይህ በንግስና ዙፋን ላይ የተቀመጠውን ፈርዖንን የመለከታል

• በወፍጮ እግር እስካለችው (ፈሊጣዊ አነጋገር)

የወፍጮ መጅ ገፊ እስከ ሆነችው ወይም በድንጋይ መፍጫ እህል በመፍጨት እስከምታገለግል

Exodus 11:6

• ከዚያም በኋላ እወጣለሁ

ሙሴ የእስራኤልን ህዝብ አስከትሎ ከግብጽ እንደሚሄድ መናገሩ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “ከዚያም በኋላ እሄዳለሁ” ወይም “እኔም ከዚያ በኋላ እሄዳለሁ”

Exodus 11:9

• ተአምራቴ በግብፅ አገር ብዙ እንዲሆን

በግብጽ ምድር ላይ ብዙ ተአምራት አደርግ ዘንድ ወይም በግብጽ ምድር ድንቅ ሥራዎቼ በብዛት እንዲታዩ

• እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ አጸና

የፈርዖን ልብ የተባለው ራሱ ፈርዖን ማለት ነው። ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም ወይም እምብ አለ ማለት ነው። (ወካይ ወይም ተለዋጭ ዘይቤ ተመልከት)። በዚህኛ ክፍል የፈርዖንን ልብ ያደነደነው ወይም ፈርዖን እንዳይሰማ ያደረገው እግዚአብሔር (ያህዌ) ነው።


Chapter 12

1 በግብፅ ምድር ለሙሴና ለአሮን እንዲህ ብሎ ነገራቸው፤ 2 ወር ለእናንተ የወሮች መጀመሪያ፣ የዓመቱም የመጀመሪያ ወር ይሁናችሁ። 3 ጉባኤ ይህን ንገሩ፤ ‘በዚህ ወር ዐሥረኛ ቀን ላይ እያንዳንዳቸው ለራሳቸው አንድ ጠቦት የሚያንስ ከሆነ፣ 4 የቅርብ ጎረቤቱ ከቊጥራቸው ጋር የሚመጣጠን ጠቦት ያዘጋጁ። የሚመገቡትን በቂ ሥጋ መውሰድ እንዲችሉ፣ ጠቦቱ ለሁሉም የሚበቃ መሆን አለበት። 5 ወይም የፍየል ጠቦታችሁ እንከን የሌለበት የአንድ ዓመት ተባት ጠቦት ሊሆን ይገባል። ከበጎቹ ወይም ከፍየሎቹ አንዱን ልትወስዱ ትችላላችሁ። 6 እስከ ወሩ ዐሥራ አራተኛ ወር ድረስ አቆዩአቸው። ከዚያም መላው የእስራኤል ጉባኤ እነዚህን እንስሳት ፀሐይ ስትጠልቅ ይረዷቸው። 7 ከዚያም ከደሙ ጥቂት ውሰዱና ሥጋውን በምትበሉበት ቤት በር መቃንና ጉበን ላይ አድርጉት። 8 በእሳት ከጠበሳችሁት በኋላ፣ በዚያው ሌሊት ከቂጣና ከመራራ ቅጠል ጋር ብሉት። 9 ወይም ቅቅሉን አትብሉት። ይልቁን ከጭንቅላቱ፣ ከእግሮቹና ከሆድ ዕቃው ጋር በእሳት ጠብሳችሁ ብሉት። 10 ድረስ ከሥጋው አንዳችም አታስቀሩ። የተራረፈ ነገር ቢኖር፣ በእሳት ይቃጠል። 11 ወገባችሁን ታጥቃችሁ፣ ጫማችሁን አጥልቃችሁና በትራችሁን በእጃችሁ ይዛችሁ ነው። ተጣድፋችሁ ልትበሉት ይገባል። የእግዚአብሔር ፋሲካ ነው። 12 በዚያ ሌሊት በግብፅ ምድር ሁሉ ዐልፋለሁ፤ በግብፅ ምድርም የሰውንና የእንስሳትን በኵር በሙሉ እመታለሁ። በግብፅ አማልክት ሁሉ ላይ እፈርድባቸዋለሁ። እኔ እግዚአብሔር ነኝ። 13 ደሙ እኔ ወደ እናንተ በቤቶቻችሁ ላይ ምልክት ይሆናል። ደሙንም በማይበት ጊዜ የግብፅን ምድር ስመታ እናንተን ዐልፌአችሁ እሄዳለሁ። ይህ መቅሠፍት በእናንተ ላይ አይመጣም፤ አያጠፋችሁምም። 14 ቀን የእግዚአብሔር በዓል ቀን አድርጋችሁ የምታከብሩት የመታሰቢያ ቀን ይሆንላችኋል። ቀኑን እንድታከብሩት ለእናንተ፣ ለትውልዶቻችሁም ሁሉ ቋሚ ሥርዐት ይሆናችኋል። 15 ቀን ቂጣ ትበላላችሁ። በመጀመሪያው ቀን እርሾውን ከቤታችሁ ታስወግዳላችሁ። ከመጀመሪያው ቀን እስከ ሰባተኛው ቀን እርሾ ያለበትን እንጀራ የበላ ሰው ሁሉ ከእስራኤል ይወገድ። 16 በመጀመሪያው ቀን ለእኔ የተቀደሰ ጉባኤ ይደረጋል፤ በሰባተኛውም ቀን እንደዚሁ ያለ ሌላ ጉባኤ ይሆናል። ሁሉም የሚበላውን ከመቀቀል በቀር፣ በእነዚህ ቀኖች ሥራ አይሠራም። የምትሠሩት የምግብ ዝግጅቱን ሥራ ብቻ ነው። 17 በዓልን አክብሩት ምክንያቱም ሕዝባችሁን ሰራዊት በሰራዊት አድርጌ ከግብፅ ምድር ያወጣሁት በዚህ ቀን ነው። ስለዚህ ይህን ቀን በትውልዶቻችሁ ሁሉ አክብሩት፤ ለእናንተ ቋሚ ሥርዓት ይሆናችኋል። 18 የመጀመሪያ ወር ዐሥራ አራተኛ ቀን ፀሐይ መጥለቅ አንሥቶ፣ እስከ ወሩ ሃያ አንደኛ ቀን ፀሐይ መጥለቅ ድረስ ቂጣ ትበላላችሁ። 19 በሰባቱ ቀኖች በቤታችሁ ውስጥ እርሾ መገኘት የለበትም። እርሾ ያለበት እንጀራ የሚበላ እንግዳም ሆነ በምድራችሁ የተወለደ ሰው ከእስራኤል ማኅበረ ሰ ይወገዳል። 20 የተጋገረ አንዳችም መብላት የለባችሁም። የትም ብትኖሩ፣ መብላት የሚገባችሁ እርሾ የሌለበትን ነው።” 21 በኋላ ሙሴ የእስራኤልን ሽማግሌዎች ሁሉ ጠርቶ እንዲህ አላቸው፤ “ሂዱና ቤተ ሰቦቻችሁን ለመመገብ የሚበቁ ጠቦቶችን ወይም ግልገሎችን መርጣችሁ የፋሲካን በግ ዕረዱ። 22 ጭብጥ የሂሶጵ ቅጠል ያዙና በሳሕን ውስጥ በሚቀመጠው ደም ውስጥ በመንከር፣ የቤታችሁን ጉበን ዐናትና ሁለቱን መቃኖች እርጩ። እስኪነጋ ድረስ ከእናንተ አንድም ከቤቱ አይወጣ። 23 ለመቅሠፍት እግዚአብሔር ስለሚያልፍ፣ ደሙን በጉበኑ ዐናትና በሁለቱ መቃኖች ላይ ሲያይ፣ በበራፋችሁ ላይ ያልፋል፣ ቀሣፊውም ወደ ቤታችሁ እንዲገባና እናንተን እንዲቀሥፋችሁ አይፈቅድም። 24 ይህ ሥርዐት ለእናንተም ለልጆቻችሁም የሁልጊዜ ሥርዐት ስለ ሆነ ልታከብሩት ይገባል። 25 ቃል በገባላችሁ መሠረት፣ እግዚአብሔር ወደሚሰጣችሁ ምድር ስትገቡ፣ ይህን የአምልኮ ሥርዐት ጠብቁት። 26 ‘ይህ የአምልኮ ሥርዐት ምን ትርጕም አለው?’ ብለው በሚጠይቋችሁ ጊዜ፣ 27 እንደዚህ ብላችሁ ልትነግሯቸው ይገባል፤ ‘ይህ የእግዚአብሔር ፋሲካ መሥዋዕት ነው፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ግብፃውያንን ሲቀሥፍ፣ በግብፅ ውስጥ በእስራኤላውያን ቤቶች ዐልፎ ሄዶአል። ቤተ ሰቦቻችንን ነጻ አውጥቷቸዋል።” ከዚያም ሕዝቡ ሰገዱ፣ እግዚአብሔርንም አመለኩት። 28 ሄደው እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን እንዳዝዛቸው አደረጉ። 29 እኩለ ሌሊት ላይ በዙፋኑ ላይ ከሚቀመጠው ከፈርዖን በኵር ልጅ ጀምሮ፣ በእስር ቤት ውስጥ እስካለው ሰው በኵር ልጅና እስከ እንስሳት በኵር ሁሉ ድረስ፣ እግዚአብሔር በግብፅ ምድር የሚገኝን በኵር በሙሉ ቀሠፈ። 30 አገልጋዮቹ ሁሉና ግብፃውያን በሙሉ ሌሊት ላይ ተነሡ። በግብፅ ውስጥ ጕልሕ የልቅሶ ጩኸት ነበረ፤ ሰው ያልሞተበት እንደም ቤት አልነበረምና። 31 ሙሴንና አሮንን በሌሊት አስጠርቶ እንዲህ አላቸው፤ “ተነሡ፤ እናንተና እስራኤላውያን ከሕዝቤ መካከል ውጡ። ማድረግ የምትፈልጉትን እንደ ተናገራችሁ ሂዱ፣ እግዚአብሔርን አምልኩ። 32 እንደ ተናገራችሁት፣ የበግና የፍየል መንጎቻችሁን፣ የቀንድና የጋማ ከብቶቻችሁንም ይዛችሁ ሂዱ፤ እኔንም ባርኩኝ።” 33 እስራኤላውያንን ከአገራቸው ለማባረር በትልቅ ጥድፊያ ላይ ነበሩ፤ “ሁላችንም ማለቃችን ነው” ብለው ነበርና። 34 ሕዝቡ እርሾ ያልተጨመረበትን ሊጣቸውን ያዙ። የቡሆ እቃዎቻቸውን ቀድሞውኑ በጨርቃቸው አስረው በትከሾቻቸው ተሸክመዋቸዋል። 35 ሕዝብ ሙሴ እንደ ነገራቸው አደረጉ። የወርቅና የብር ዕቃዎችን፣ ልብስም እንዲሰጧቸው ግብፃውያንን ጠየቁ። 36 ደስ ለማሰኘት እግዚአብሔር ግብፃውያንን አነሣሣ። ስለዚህ እስራኤላውያን የጠየቋቸውን ሁሉ ግብፃውያን ሰጧቸው። በዚህ መንገድ፣ እስራኤላውያን ግብፃውያንን በዘበዟቸው። 37 ከራምሴ በመነሣት ወደ ሱኮት ተጓዙ። ቊጥራቸው ከሕፃናቱና ከሴቶቹ ሌላ ስድስት መቶ ሺሕ ያህል እግረኛ ነበር። 38 እስራኤላዊ ያልሆነ ድብልቅ ሕዝቤም፣ ከበግና ከፍየል፣ እጅግ ብዙ ከሆነ የከብት መንጋ ጋር ዐብሯቸው ሄደ። 39 ከግብፅ ያመጡትን እርሾ ተባርረው ስለ ወጡና ምግብ ማዘጋጀት ስላልቻሉ ነው። 40 እስራኤላውያን በግብፅ ውስጥ የኖሩት አራት መቶ ሠላሳ ዓመት ነበር። 41 መቶ ሠላሳው ዓመት ፍጻሜ፣ በዚያው ቀን፣ ሁሉም የእግዚአብሔር ሰራዊት ከግብፅ ምድር ወጣ። 42 ሌሊት እግዚአብሔር ከግብፅ ምድር እንዲያወጣቸው ለእስራኤላውያን ነቅቶ የመቆያ ሌሊት ነበር። ይህ ሌሊት እስራኤላውያን ሁሉ፣ መላ ትውልዶቻቸው ሊያከብሩት የሚገባ ሌሊት ነው። 43 እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፤ “የፋሲካ ሕግ እነሆ፦ ባዕድ ሰው ፋሲካን አይበላውም። 44 የተገዛ እያንዳንዱ የእስራኤል ባሪያ ግን ከገረዛችሁት በኋላ መብላት ይችላል። 45 ቅጥር አገልጋዮች መብላት አይገባቸውም። 46 ምግቡ በአንድ ቤት ውስጥ መበላት አለበት። ሥጋ ከቤት ማውጣት፣ ዐጥንትም መስበር የለባችሁም። 47 የእስራኤል ማኅበረ ሰብ በዓሉን ሊያከብር ይገባል። 48 ባዕድ ሰው ከእናንተ ጋር ቢኖርና ፋሲካን ለእግዚአብሔር ለማክበር ቢፈልግ፣ ወንድ ዘመዶቹ ሁሉ መገረዝ አለባቸው። ከዚያም በኋላ፣ ሰውየው መምጣትና በዓሉን ማክበር ይችላል። በምድሩ እንደ ተወለዱት ሰዎች ይሆናል። ይሁን እንጂ፣ ያልተገረዘ ሰው የፋሲካን ምግብ አይበላም። 49 አንድ ዐይነት ሕግ ተግባራዊ የሚሆነው በሁለቱም ማለት በአገሬው ተወላጅና በመካከላችሁ በሚኖረው ባዕድ ሰውም ላይ ነው።” 50 እስራኤላውያን ሁሉ እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን እንዳዘዛቸው አደረጉ። 51 በዚያው ቀን እግዚአብሔር እስራኤላውያንን በየሰራዊታቸው ከግብፅ ምድር አወጣቸው።



Exodus 12:1

• ይህ ወር የወሮች መጀመሪያ ይሁናችሁ፣ የዓመቱም መጀመሪያ ወር ይሁናችሁ

እነዚህ ሁለት ሀረጎች በመሰረቱ አንድ ትርጉም ወይም ፍቺ ያላቸው ሲሆን አጽንዖት ለመስጠት የገባ በመሆኑ እስራኤላውያን ከግብጽ የወጡበትንና አዲስ ታሪክ የጀመረበት ስለሆነ ወሩ የአመቱ መጀመሪያ ወር እንዲሆንላቸው የተነገረ ወይም የተሰጠ ነው። ይህ ወር የሚጀምረው በአመዛኙ በሚያዚያ ወር አከባቢ ነው።

Exodus 12:3

• የቤቱ ሰዎች ቁጥርም ለጠቦቱ የማይበቃ ቢሆን

በአንድ ቤተሰብ ውስጥ ያሉ ሰዎች ቁጥር አንድን የበግ ጠቦት በልቶ ለመጨረስ የማይበቃ ከሆነ

• እርሱና ለቤቱ የቀረበው ጎረቤቱ

“እርሱ” የተባለው የዚያ ቤተሰብ መሪ የሆነው ሰው ማለት ነው

Exodus 12:5

• ሲመሽ

“ምሽት” የሚለው ቃል ሙሉ በሙሉ ሲመሽ ሳይሆን ፀሐይ መጥለቂያ እና ማምሻ መካከል ያለው ሰዓት ሲሆን ከመጨለሙ በፊት ብርሃን ያለ መሆኑን አመልካቺ ነው።

• መቃን ጉበኑን ይቅቡት

የበሩን ወይም የደጃፉን ጎንና ጎን እንዲሁም የላኛውን ጉበን ማለት ነው።

• ቂጣውን እንጀራ

በአማርኛ “ቂጣ እንጀራ” ወይም “እንጀራ ቂጣ” ምን ማለት እንደሆነ ግልጽ ላይሆን ይችላል። ቂጣውን እንጀራ ማለት እርሾ ያልገባበት ደረቅ ቂጣ ሲሆን እንደ ህብረተሰቡ አጠቃቀም “ቂጣ፥ ያልቦካ ቂጣ፥ ደረቅ ቂጣ” ሊሆን ይችላል።

• ከመራራ ቅጠል ጋር ይበሉታል

መራራ ቅጠል የተባለው ምን ዓይነት ተክል እንደሆነ በስም አልተገለጸም። በአይሁዳውያን ባህል ሥጋ ለማድረቅ ወይም ለመቀመም የሚጠቀሙበት ተክል ዓይነት ነው።

Exodus 12:9

• ጥሬውን በውኃም የበሰለውን አትብሉ

የፍየሉን ወይም የበጉን ጥሬ ሥጋ ወይም በውሃ ተቀቅሎ የበሰለውን አትብሉ

• ከእርሱም እስከ ጥዋት አንዳች አታስቀሩ

ከሥጋው እስከ ጧት ድረስ ምንም አታስቀሩ

• ወገቦቻችሁን ታጥቃችሁ

የወገብ መታጠቂያ ከቆዳ ወይም ከጥጥ የተሰራ የወገብ መታጠቂያ ወይም በእያንዳንዱ ባህል ማህበረሰቡ የሚጠቀመው የወገብ መታጠቂያ ሊሆን ይችላል።

• ፈጥናችሁም ትበሉታላችህ

በጥድፊያ ወይም በችኮላ ብሉት

• እርሱ የእግዚአብሔር ፋሲካ ነው

“እርሱ” የሚለው በአስራ አራተኛው ቀን የበግ ወይም ፍዬል ጥቦት እረድና የመብላት ሥርዓቱን ማለት ነው።

Exodus 12:12

• በግብፅም አማልክት ሁሉ ላይ እፈርድባቸዋለሁ

የግብጽን አማልክት ወይም እግዚአብሔሮች ሁሉ እቀጣለሁ

• ደሙም ባላችሁበት ቤቶች ምልክት ይሆንላችኋል

እኔ ወደ እናንተ በሚመጣበት ጊዜ ደሙ የእስስራኤላውያን ቤት ስለመሆኑ ምልክት ይሆንልኛል።

• ደሙንም ባየሁ ጊዜ ከእናንተ አልፋለሁ

እኔም ደሙን በማይበት ጊዜ አልፌአችሁ እሄዳለሁ ወይም ወደ ቤታችሁ ሳልገባ/ሳልጎበኛችሁ አልፌ እሄዳለሁ (ዘይቤያዊ ንግግር)

• ለልጅ ልጃችሁ ሥርዓት ሆኖ ለዘላለም ታደርጉታላችሁ

በሚቀጥሉት ትውልዶች ወይም ዘመናት ሁሉ ቋሚ ሥርዐት ሆኖ የእግዚአብሔር (ያህዌ) በዓል አድርጋችሁ ታከብሩታላችሁ።

Exodus 12:15

• ማንኛውም ሰው ከእስራኤል ይጥፋ

“ይጥፋ” የሚለው ዘይቤያዊ አነጋገር ሶስት አማራጭ ፍቾች ይኖሩታል። 1) የእስራኤል ሰዎች ይህን ሰው ከመካከላቸው አውጥተው ማስወገድ አለባቸው 2) ይህ ሰው ከእስራኤላውያን እንደ አንዱ መታየት የለበትም 3) እስራኤላውያን ይህን ሰው መግደል ወይም ማጥፋት አለባቸው።

• በመጀመሪያውም ቀን የተቀደሰ ጉባኤ እንዲሁም በሰባተኛውም ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ይሆንላችኋል

በመጀመሪያውና በሰባተኛው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ታደርጋላችሁ

• ከሚበላ በቀር በእነርሱም ምንም አትሠሩም

በእነዚያም ቀኖች ምግባችሁን ከማዘጋጀት በቀር ምንም ሥራ አትሠሩም

• ይህንም ብቻ ታደርጉታላችሁ

የምትሠሩት ሥራ ቢኖር ለእያንዳንዱ ምግብ ማዘጋጀት ብቻ ይሆናል።

Exodus 12:17

• ሠራዊታችሁን ከግብፅ አገር አውጥቼአለሁና

ይህ አገላለጽ ለጦር ሠራዊት የተሰጠ ስም ሲሆን በዚህ ክፍል የተገለጸው “ክፍል ለክፍል ወይም ቡድን ለቡድን” በሰልፍ የሚወጣውን የእስራኤልን ህዝብ የሚመለከት ነው።

• ሲመሽ

“ምሽት” የሚለው ቃል ሙሉ በሙሉ ሲመሽ ሳይሆን ፀሐይ መጥለቂያ እና ማምሻ መካከል ያለው ሰዓት ሲሆን ከመጨለሙ በፊት ብርሃን ያለ ማለት ነው።

• በመጀመሪያውም ወር በአሥራ አራተኛው ቀን

ይህ ወር በእስራኤላውያን ዘመን አቆጣጠር የአመቱ የመጀመሪያ ወር ነው። በአውሮጳውያን አቆጣጠር የመጋቢት መጨረሻ ሳምንት እና የሚያዚያ የመጀመሪያ ሳምንት አከባቢ የሚጀምር ወር ነው።

• ከወሩም እስከ ሀያ አንድ ቀን በመሸ ጊዜ

የመጀመሪያ ወር በገባ በ21ኛው ቀን ማለት ነው

Exodus 12:19

• ሰባት ቀን በቤታችሁ እርሾ አይገኝ

እስከ ሰባት ቀን ድረስ ምንም ዓይነት እርሾ በቤታችሁ መገኘት የለበትም

• ከእስራኤል ማኅበር ተለይቶ ይጥፋ

ዘጸአት 12፡15 ተመልከት

• እርሾ ያለበትን ምንም አትብሉ

ዘጸአት 12፡5-8 ያለውን ማብራሪያ ተመልከት

Exodus 12:21

• ሂሶጵ

ሸካራ የሆነ ትናንሽ ቅጠሎች ያሉት በተለይ ፈሳሽ ነገሮችን ለመርጨት የሚያገለግል የዛፍ ዓይነት ነው

• መቃኖችና ጉበኑን እርጩ

የበሩን ወይም የደጃፉን ጎንና ጎን እንዲሁም የላኛውን ጉበን ማለት ነው።

Exodus 12:23

• እግዚአብሔር በደጁ ላይ ያልፋል

“በደጁ” ላይ ያልፋል የሚለው ጠቅላላውን ቤተሰብ ወይም ቤት የሚመለከት ነው። ደም በመቃኖቻቸውና በጉበኖቻቸው ላይ የተገኘባቸው ቤቶችን እግዚአብሔር ሳይነካቸው ያልፋል ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር ቤታችሁን ትቶ ያልፋል

Exodus 12:24

• ይህችን ነገር ጠብቁ

“ይህችን ነገር” የተባለው “የፋሲካ በዓል” ወይም “የቂጣ በዓል” ማለት ነው። የፋሲካ በዓል ማክበር እግዚአብሔኤርን (ያህዌን” ማክበር ነው።

Exodus 12:26

• ቤቶቻችንን ያዳነ የእግዚአብሔር የማለፉ

በሌላ አገላለጽ፦ እግዚአብሔር የእስራኤላውያንን መኖሪያ ቤቶች አልፎ በመሄድ ቤታቸውን ስላተረፈ ወይም በእስራኤላውያን ቤት የሚገኙትን በኩር ወንድ ልጆችን ባለመግደሉ”

• እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን እንዳዘዘ እንዲሁ አደረጉ

ሄደውም በሙሴና በአሮን አማካይነት እግዚአብሔር ያዘዛቸውን ሁሉ አደረጉ

Exodus 12:29

• በዙፋን ከተቀመጠው ከፈርዖን በኵር ጀምሮ በግዞት እስካሉት እስከ ምርኮኞቹ በኵር ድረስ

በኩር የሚለው ቃል ሁል ጊዜ መጀመሪያ የተወለደን ወንድ (ሰውና እንስሳ) የሚመለከት ነው። (ዘጸአት 11፡5 ተመልከት)

• በዙፋን ከተቀመጠው ከፈርዖን በኵር ጀምሮ

በዙፋን ላይ ከተቀመጠው ከፈርዖን የበኵር ልጅ ጀምሮ

• በግዞት እስካሉት እስከ ምርኮኞቹ በኵር ድረስ

በጨለማ እስር ቤት ውስጥ እስካለው እስረኛ የበኵር ልጅ ድረስ ያለውን ማለት ነው። ምርኮኛ የተባለው አንድ እስረኛ ሳይሆን ሁሉንም እስረኛ ሲሆን አንደ አንድ ሰው የተጠቀሰው ለሁሉም ያገለግላል ማለት ነው።

• የሞተ የሌለበት ቤት አልነበረምና

በኩር የሆነ ወንድ ልጅ ያልሞተበት አንድ ቤት እንኳ አልነበረም

• በግብፅ ምድር ታላቅ ልቅሶ ሆነ

በግብጽ ምድር ሁሉ ታላቅ የለቅሶ ጩኸትና ዋይታ ሆነ

Exodus 12:31

• ሁላችን እንሞታለን ብለዋልና

እስራኤላውያን ግብጽን ለቀው ካልወጡ ሁላችን እናልቃለን ብለው ግብጻውያን ስለፈሩ ---። አማራጭ ትርጉም፦ “እናንተ ለቃችሁ የማትሄዱ ከሆነ እኛም መሞታችን ነው”

Exodus 12:34

• ሕዝቡም ሊጡን ሳይቦካ ተሸከሙ፥ ቡሃቃውንም በልብሳቸው ጠቅልለው በትከሻቸው ተሸከሙት

በሌላ አገላለጽ፦ ሕዝቡ ያልቦካውን ሊጥ በየቡሆ ዕቃው አድርገው በጨርቅ ጠቅልለው በትከሻቸው ተሸከሙ

Exodus 12:37

• ከራምሴ

ራምሴ ግብጻውያን እህል ከሚያከማቹባቸው ከተሞች አንዱ ነው። (ዘጸአት 1፡11 ተመልከት)

• ከሕፃናቱም ሌላ ስድስት መቶ ሺህ ሰው የሚያህል እግረኛ ነበረ

“ህጻናት” የተባሉት ድጋፍ የሚፈልጉ ወንድና ሴት ልጆችን የሚመለከት ወይም ህጻናትና ሴቶችን የሚመለከት ሊሆን ይችላል። ጠቅላላ መዋጋት የሚችሉ ወንዶች ብዛት ስድስት መቶ ሺህ ያህል ነበር።

• ከግብፅም ከእነርሱ ጋር ያወጡትን ሊጥ ጋገሩ

ከግብፅ ይዘው ከወጡት ሊጥ ያልቦካ ቂጣ ጋገሩ

• ግብፃውያን በመውጣት ስላስቸኮሉአቸው ይቆዩ ዘንድ አልተቻላቸውም

ከግብፅ በጥድፊያ ወይም በችኮላ እንዲወጡ ስለተደረጉ ለራሳቸው ምግብ ለማዘጋጀት ጊዜ አልነበራቸውም

Exodus 12:41

• የእስራኤልም ልጆች በግብፅ ምድር የተቀመጡት ዘመን አራት መቶ ሠላሳ ዓመት ነው

እስራኤላውያን በግብጽ ምድር የኖሩት አራት መቶ ሠላሳ ዓመት ነበር

• የእግዚአብሔር ሠራዊት ሁሉ ከግብፅ ምድር ወጣ

እዚህ ጋር ሠራዊት የተባለው የእስራኤልን ህዝብ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “የእግዚአብሔር ሕዝብ ሁሉ የግብጽን ምድር ለቆ ወጣ” (ዘጸአት 12፡17 ተመልከት)

• በእስራኤል ልጆች ሁሉ ዘንድ እስከ ልጅ ልጃቸው ድረስ ለእግዚአብሔር የተጠበቀች ናት

ይህ ሌሊት እስራኤላውያን በመጠባበቅ ተግተው የሚያድሩበትና ለሚመጣው ትውልድ ወይም ዘመን ሁሉ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ሌሊት ነው

Exodus 12:43

• ከእርሱ እንግዳ ሰው አይብላ

“እርሱ” የተባለው የፋሲክን ምግብ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የባዕድ አገር ሰው የሆነ የፋሲካን ራት ወይም ምግብ አይብላ

• በብር የተገዛ ባሪያ ቢኖር

በገንዘብ የገዛችሁት ማንኛውም ባሪያ ቢሆን

Exodus 12:45

• በአንድ ቤትም ይበላ

ምግቡ በሙሉ በዚያው በተዘጋጀበት ቤት ውስጥ መበላት አለበት ማለት ነው

• አጥንትም አትስበሩት

የሚታረደው ጠቦት አጥንቶቹን አትስበሩ

Exodus 12:47

• አስቀድሞ ወንድ ሁሉ ይገረዝ

አስቀድማችሁ በቤተሰቡ ያሉትን ወንዶች ሁሉ ግረዙ

• ያልተገረዘ ሁሉ ግን ከእርሱ አይብላ

በሌላ አባባል የተገረዘ ሁሉ ከፋሲካው ምግብ መብላት ይችላል ማለት ነው

Exodus 12:49

• እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን እንዳዘዘ እንዲሁ አደረጉ

እግዚአብሔር በሙሴና በአሮን አማካይነት ያዘዘውን ሁሉ ፈጸሙ

• የእስራኤልን ልጆች ከሠራዊታቸው ጋር (ዘጸአት 12፡17 ተመልከት)

አማራጭ ትርጉም፦ “እግዚአብሔር መላውን የእስራኤል ሕዝብ በክፍል በክፍል ከግብጽ ምድር መርቶ አወጣ”


Chapter 13

1 ሙሴን እንዲህ አለው፤ 2 ‘በእስራኤላውያን ዘንድ ከሰውም ሆነ ከእንስሳት በመጀመሪያ የተወለደውን ወንድ ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ። በኵር የእኔ ነው።” 3 ለሕዝቡ እንዲህ አለ፤ “ከባርነት ቤት ከግብፅ የወጣችሁበትን ይህን ቀን አስታውሱት፤ በዚህ ቀን እግዚአብሔር በብርቱ እጁ ከዚህ ስፍራ አውጥቶአችኋልና። እርሾ ያለበት ምግብ አይበላም። 4 በዚህ ቀን፣ በአቢብ ወር ከግብፅ ወጥቷችኋል። 5 ለእናንተ ለመስጠት ለአባቶቻችሁ ወደ ማለላቸው፣ ማርና ወተት ወደምታፈስሰው፣ ወደ ከነዓናውያን፣ ኬጢያውያን፣ አሞራውያን፣ ኤውያውያን፣ ኢያቡሳውያን ምድር እግዚአብሔር ሲያስገባችሁ፣ ይህን አምልኮ በዚህ ወር ትፈጽማላችሁ። 6 ቀን ቂጣ ትበላላችሁ፤ በሰባተኛውም ቀን እግዚአብሔርን የምታከብሩበት በዓል ይሆናል። 7 ቀን ሁሉ መበላት ያለበት ቂጣ ነው፤ እርሾ ያለበት እንጀራ በእናንተ ዘንድ መታየት የለበትም። በአዋሳኞቻችሁም ዘንድ እርሾ አይኑር። 8 ቀን፣ ‘ይህ እንዲህ የሚሆነው ከግብፅ ስወጣ እግዚአብሔር ለእኔ ካደረገው የተነሣ ነው’ ብላችሁ ለልጆቻችሁ ትነግሯቸዋላችሁ።’ 9 ይህም በእጃችሁና በግንባራችሁ ላይ መታሰቢያ ይሆናል። ይኸውም እግዚአብሔር በብርቱ እጁ ከግብፅ ስላወጣችሁ፣ የእግዚአብሔር ሕግ በአፋችሁ እንዲሆን ነው። 10 ይህን ሕግ በየዓመቱ በተወሰነለት ጊዜ ልትጠብቁት ይገባል። 11 ለእናንተና ለአባቶቻችሁ በማለው መሠረት፣ እግዚአብሔር ወደ ከነዓናውያን ምድር ሲያስገባችሁ፣ 12 በመጀመሪያ የተወሰደውን፣ የእንስሶቻችሁንም በኵር ሁሉ ለእግዚአብሔር ቀድሱ። ወንዶች የእግዚአብሔር ናቸው። 13 ከአህያ በመጀመሪያ የተወለደውን ሁሉ በጠቦት ትዋጁታላችሁ። ካልዋጃችሁት፣ ዐንገቱን ስበሩት። ከወንድ ልጆቻችሁ መካከል በኵር የሆኑትን ሁሉ ዋጇቸው። 14 ልጅህ፣ ‘ይህ ምን ማለት ነው? ብሎ ወደፊት ቢጠይቅህ፣ እንደዚህ ትነግረዋለህ ‘ከባርነት ቤት፣ ከግብፅ እግዚአብሔር ያወጣን በብርቱ እጅ ነበር። 15 እኛን ለመልቀቅ በግትርነት እንቢ ባለ ጊዜ፣ እግዚአብሔር በግብፅ ምድር ያለውን በኵር ሁሉ፣ የሰውንም ሆነ የእንስሳትን በኵር በሙሉ ገደለ። ከእንስሳት ሁሉ በመጀመሪያ የተወለደውን ለእግዚአብሔር የምሠዋውና ከወንድ ልጆችም በኵር የሆነውን የምዋጀውን በዚህ ምክንያት ነው።’ 16 ከግብፅ ያወጣን በብርቱ እጅ ነውና፣ ይህ በእጅህና በግንባር ላይ ማስታወሻ ይሆናል።” 17 ሕዝቡን ሲለቅቃቸው፣ እግዚአብሔር ምንም እንኳ ቅርብ ቢሆንም፣ በፍልስጥኤማውያን ምድር ባለው መንገድ አልመራቸውም። እግዚአብሔር፣ “ሕዝብ ጦርነት ቢያጋጥማቸው፥ ምናልባት ሐሳባቸውን ይለውጣሉ፣ ወደ ግብፅም ይመለሳሉ” ብሎ ነበርና። 18 እግዚአብሔር ሕዝቡን በምድረ በዳው ዙሪያ ውደ ቀይ ባሕር መራቸው። እስራኤላውያን ለውጊያ ተዘጋጅተው ከግብፅ ምድር ወጥተው ሄዱ፣ 19 ሙሴ የዮሴፍን ዐፅም ይዞ ሄደ፤ ምክንያቱም ዮሴፍ፣ “እግዚአብሔር በእርግጥ ይታደጋችኋልና ዐፅሜን ይዛችሁ እንድትሄዱ” በማለት እስራኤላውያንን አስምሎአቸው ነበር። 20 ከሱኮት በመጓዝ ምድረ በዳው ዳር ላይ በሚገኘው በአታም ሰፈሩ። 21 እግዚአብሔር ሕዝቡን በመንገድ ላይ ሊመራቸው ቀን ቀን በደመና ዐምድ በፊታቸው ሄደ። ሌሊት ሌሊት ደግሞ ብርሃን ሊሰጣቸው በእሳት ዐምድ ሄደ። በዚህ ዐይነት ሕዝቡ በቀንም በሌሊትም መጓዝ ቻሉ። 22 እግዚአብሔር የቀኑን የደመና ዐምድ ወይም የሌሊቱን የብርሃን ዐምድ ከሕዝቡ ፊት አላነሣም።



Exodus 13:1

• ማሕፀንን የሚከፈት በኵር ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ

በኲር ሆኖ የተወለደ ሁሉ ለእግዚአብሔር የተለየ እንዲሆን እግዚአብሔር ይፈልገዋል

Exodus 13:3

• ይህን ቀን አስቡ

“ይህን ቀን አስቡ” የሚለው አንድ ሰው ያለፈውን ነገር ወደ ኋላ እንዲያስታውስ መናገር የተለመደ አባባል ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ይህን ቀን አስታውሱ ወይም ይህን ቀን አትርሱ።

• የባርነት ቤት

ህዝቡ በአንድ ቤት ታጉሮ እንደነበር ዓይነት አነጋገር የያዘ ዘይቤ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “በባርነት የነበራችሁበት ዘመን ወይም ሁኔታ”

• እግዚአብሔር . . . በብርቱ እጅ አውጥቶአችኋልና

ምክንያቱም እግዚአብሔር በታላቅ ኀይሉ በመታደግ አውጥቷችኋል

• የቦካ እንጀራ አትብሉ

እርሾ የገባበትን ዳቦ ወይም ምግብ አትብሉ

• በአቢብ ወር ወጥታችኋል

የአቢብ ወር ለእብራውያን የአመቱ መጀመሪያ ወር ነው። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር አቢብ ወር የሚጀምረው ከመጋቢት መጨረሻ ሳምንት እስከ ሚያዝያ መጀመሪያ ሳምንት ባለው ጊዜ ውስጥ ነው።

• ወተትና ማር ወደምታፈስስ ምድር

ይህ ሐረግ በግነታዊ እና በተለዋጭ ዘይቤ የተገለጸ ነው። ይህ አገላለጽ ከምድሪቱ ወተትና ማር ይፈልቃል ማለት ሳይሆን ለከብት ርባታና ለእርሻ በጣም ምቹ የሆነ ምድር እንደሆነ ለማሳየት ነው። እንዲሁም “የምታፈስ” አገር የሚለው ቃልም ሁሉም ነገር የሞላባት ምድር የሚል ፍቺ ያለው ነው።

• ይህችን አምልኮ በዚህ ወር ታደርጋለህ

እስራኤላውያን በከነዓን ሲኖሩ በዓመቱ መጀመሪያ ወር ላይ ይህን በዓል (የፋሲካ በዓል) ማክበር አለባቸው (ዘጸአት 12፡25)

Exodus 13:6

አጠቃላይ ምልከታ፦ ሙሴ ለእስራኤል ሰዎች አሁንም ቀጥሎ ይናገራል • ሰባት ቀን ቂጣ እንጀራ ትበላለህ

እስከ ሰባት ቀን ወይም ለሰባት ቀን ሙሉ እርሾ ያልገባበትን ምግብ ትበላላችሁ

• በአንተም ዘንድ እርሾ ያለበት እንጀራ አይታይ

እርሾም ሆነ እርሾ የገባበት ምግብ በፍጹም በምድራችሁ አይገኝ

• በድንበርህም ሁሉ እርሾ አይታይ

እርሾ በአገርህ ውስጥ በየትኛውም ሥፍራ/ቦታ/ አይገኝ

Exodus 13:8

• በዚያም ቀን፦ ከግብፅ በወጣሁ ጊዜ እግዚአብሔር ስላደረገልኝ ነው ስትል ለልጅህ ትነግረዋለህ

ይህ አነጋገር በቀጥታ አነጋገር ሲገለጽ፦ “በዓሉን በምታከብርበት ወቅት ይህን የምታደርገው ከግብጽ በወጣህበት ጊዜ እግዚአብሔር ያደረገልህን መልካም ነገር ለማስታወስ መሆኑን ለልጆችህ ንገራቸው”

• በብርቱ እጅ ከግብፅ አውጥቶሃልና

ምክንያቱም እግዚአብሔር በታላቅ ኀይሉ ከግብጽ አውጥቷችኋል

• በእጅህ እንደ ምልክት በዓይኖችህም መካከል እንደ መታሰቢያ ይሁንልህ

እስራኤላውያን በዓሉን ወይም የፋሲካን በዓል ሲያከብሩ እነዚህን ሁለት የሚታዩ ምልክቶችን እንድያደርጉ ሙሴ ያሳስባቸዋል።

• በእጅህ እንደ ምልክት

ሙሴ ሲናገር እስራኤላውያን በዓሉን ሲያከብሩ በእጃቸው የሆነ ነገር አስረው እንደምያከብሩ አድርጎ ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ ለምልከነት በእጅህ ላይ የሆነ ነገር እንደምታስረው ይሁን።

• በዓይኖችህም መካከል እንደ መታሰቢያ ይሁንልህ

ሙሴ ሲናገር እስራኤላውያን በዓሉን ሲያከብሩ በግንባራቸው የሆነ ነገር አስረው እንደምያከብሩ አድርጎ ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ ለምልክትነት በግንባርህ ላይ የሆነ ነገር እንደምታስረው ይሁን።

• በብርቱ እጅ ከግብፅ አውጥቶሃልና

ምክንያቱም እግዚአብሔር በታላቅ ኀይሉ ከግብጽ አውጥቷችኋል

Exodus 13:11

• እርስዋንም በሰጠህ ጊዜ

እግዚአብሔር የከነዓናውያንን ምድር ለአንተ በሰጠህ ጊዜ

• የአህያውን በኵር በጠቦት ትዋጀዋለህ፥ ባትዋጀውም አንገቱን ትሰብረዋለህ

በኩር የተወለደ አህያ ለእግዚአብሔር አይለይም ወይም አይቀደስም። አማራጭ ትርጉም፦ በኩር የተወለደ አህያ የበግ ጠቦት በመተካት ከእግዚአብሔር ትዋጃለህ /መልሰህ ተገዛለህ/፤ ነገር ግን አህያውን መዋጀት ካልፈለግህ አንገቱን ስበረው።

• የሰውንም በኵር ሁሉ ከልጆችህ መካከል ትዋጀዋለህ

በኩር ሆኖ የተወለደን ወንድ ልጅ ሁሉ መዋጀት /መልሰህ መግዛት/ ይገባሃል

Exodus 13:14

• በሚመጣው ጊዜ ልጅህ፦ ይህ ምንድር ነው? ብሎ በጠየቀህ ጊዜ እንዲህ ትለዋለህ

በሌላ አገላለጽ፦ “በሚመጡት ዘመናት ልጆችህ የዚህ ሥርዓት ትርጉም ምንድን ነው” ብለው ቢጠይቁህ፥ እንዲህ ብለህ ታስረዳቸዋለህ

• እግዚአብሔር በብርቱ እጅ

ምክንያቱም እግዚአብሔር በታላቅ ኀይሉ

• የባርነት ቤት

ህዝቡ በአንድ ቤት ታጉሮ እንደነበር ዓይነት አነጋገር የያዘ ዘይቤ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “በባርነት የነበራችሁበትን ሁኔታ ወይም ሕይወት”

• በእጅህ እንደ ምልክት፥ በዓይኖችህም መካከል እንደ ተንጠለጠለ ነገር ይሁንልህ

እስራኤላውያን በዓሉን ወይም የፋሲካ በዓል ሲያከብሩ እነዚህን ሁለት የሚታዩ ምልክቶችን እንድያደርጉ ሙሴ ያሳስባቸዋል (ተነጻጻሪ ዘይቤ፤ ለተመሳሳይ አገላለጽ 13፡8-10 ተመልከት)

Exodus 13:17

• ምንም ቅርብ ቢሆን

ቅርብ በሆነው መንገድ

• ሕዝቡ ሰልፉን ባየ ጊዜ እንዳይጸጽተው ወደ ግብፅም እንዳይመለስ ብሎአልና

እስራኤላውያን ረጅሙን ዕድሜያቸውን በባርነት ስላሳለፉ ከጦርነት ይልቅ ሰላምን ስለሚፈልጉ ከመዋጋት ይልቅ ወደ ባርነት መመለስ ይፈልጋሉ

Exodus 13:19

• በምድረ በዳውም ዳር በኤታም ሰፈሩ

ኤታም ወደ ፍልስጥኤም በሚወስደው መንገድ ላይ በምድረ በዳው ዳር ላይ ወይም ድንበር ላይ ይገኛል

• መንገድ ሊያሳያቸው ቀን በደመና ዓምድ፥ ሊያበራላቸውም ሌሊት በእሳት ዓምድ

እግዚአብሔር ቀን በደመና ዐምድ /ምሶሶ መሳይ/፥ ሌሊት ብርሃን በሚሰጥ በእሳት ዐምድ /ምሶሶ መሳይ/ ይመራቸው ነበር


Chapter 14

1 ለሙሴ እንዲህ ብሎ ተናገር፤ 2 በሚግዶልና በባሕሩ መካከል ባለው በፊሀሒሮት ፊት፣ በበኣልዛፎንም አንጻር እንዲሰፍሩ ለእስራኤላውያን ንገር። በፊሀሒሮት ትይዩ በባሕሩ አጠገብ ትሰፍራላችሁ። 3 ፈርዖን ስለ እስራኤላውያን፣ ‘በምድሪቱ እየተንከራተቱ ነው፤ ምድረ በዳውም ዘግቶባቸዋል’ ይላል። 4 የፈርዖንን ልብ እኔ አደነድነዋለሁ፤ እርሱም እስራኤላውያንን ይከታተላቸዋል። በፈርዖንና በመላው ሰራዊቱ ምክንያት እኔ እከብራለሁ። ግብፃውያን እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ።” ስለዚህ እስራኤላውያን በተነገራቸው መሠረት ሰፈሩ። 5 ንጉሥ እስራኤላውያን እንደ ሄዱ ሲነገረው፣ ፈርዖንና አገልጋዮቹ ሐሳባቸውን በመለወጥ፣ እስራኤላውያን ለእኛ ከመሥራት ነጻ ሆነው እንዲሄዱ መፍቀዳችን ምን ማድረጋችን ነው? አሉ። 6 ሠረገላዎቹ እንዲዘጋጁለት አደረገ፤ ሰራዊቱንም ከእርሱ ጋር ይዞ ሄደ። 7 መቶ ምርጥ ሠረገሎችንና የግብፅን ሌሎች ሠረገሎች በሙሉ፣ በያንዳንዳቸው ላይ መኮንኖች ያሉባቸውን ይዞ ተንቀሳቀሰ። 8 እግዚአብሔር የግብፅን ንጉሥ፣ የፈርዖንን ልብ ስላደነደነው፣ ንጉሡ እስራኤላውያንን ተከታተላቸው። አሁን እስራኤላውያን በድል ወጥተው ሄደዋል። 9 ነገር ግን ግብፃውያን፣ ሁሉም የፈርዖን ፈረሶችና ሠረገሎች፣ የፈርዖን ፈረሰኞችና ሰራዊቱ እስራኤላውያንን አሳደዷቸው። በበኣልዛፎን አንጻር በባሕሩ አጠገብ ፊሀሒሮት ጥግ ሰፍረው እንዳሉ ደረሱባቸው። 10 ፈርዖን በቀረ ጊዜ፣ እስራኤላውያን ወደ ላይ ተመለከቱ፣ ተደነቁም። ግብፃውያን ከኋላ እየተከተሏቸው ነበርና ፈሩ። እስራኤላውያን ወደ እግዚአብሔር ጮኹ። 11 እንዲህ አሉት፤ “እዚህ ያመጣኸንና በምድረ በዳ እንድንሞት ያደረግኸው በግብፅ መቃብር ታጥቶ ይህን ነግረንህ አልነበረምን? 12 ሠራተኞች እንድንሆን ተወን’ ብለንህ ነበር። በምድረ በዳ ከምንሞት፣ ለእነርሱ ሠራተኞች ሆነን ብንቀር ይሻል ነበር።’” 13 እንዲህ አላቸው፤ “አትፍሩ። ጸንታችሁ ቁሙና ዛሬ እግዚአብሔር ለእናንተ የሚያደርግላችሁን ትድግና ታያላችሁ። ዛሬ የምታዩአቸውን ግብፃውያንን ዳግም አታዩአቸውም። 14 እግዚአብሔር ለእናንተ ይዋጋል፤ እናንተ መታገሥ ብቻ ነው ያለባችሁ።” 15 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ “አንተ ሙሴ ለምን ትጮኽብኛለህ? እስራኤላውያን ወደ ፊት እንዲሄዱ ንገራቸው። 16 የእስራኤል ስዎች በባሕሩ ውስጥ በደረቅ መሬት እንዲሻገሩ በትርህን አንሣና እጅህን በባሕሩ ላይ ዘርግተህ ለሁለት ክፈለው። 17 ተከትለዋቸው እንዲገቡ እኔ የግብፃውያንን ልብ የማደነድን መሆኔን ዕወቅ። ከፈርዖንና ከሰራዊቱ ሁሉ፣ ከሠረገሎቹና ከፈረሰኞቹ የተነሣ እኔ እከብራለሁ። 18 በፈርዖን፣ ሠረገሎቹና በፈረሰኞቹ ምክንያት ክብርን ሳገኝ፣ ግብፃውያኑ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን ያውቃሉ።” 19 ፊት ይሄድ የነበረው የእግዚአብሔር መልአክ በስተ ኋላቸው ሄደ። የደመናውም ዐምድ ከፊታቸው ተንቀሳቅሶ በስተኋላቸው ሄዶ ቆመ። 20 በግብፅ ሰራዊትና በእስራኤል መካከል መጣ። ለግብፃውያን የጨለማ ደመና ሲሆን፣ ለእስራኤላውያን ግን ሌሊቱን ብሩህ ያደረገ ደመና ነበር፤ ይህም ሌሊቱን ሙሉ አንደኛው ወገን ወደ ሌላው እንዳይጠጋ አደረገ። 21 እጁን በባሕሩ ላይ ዘረጋ። እግዚአብሔርም በዚያ ሌሊት ባሕሩን በብርቱ የምሥራቅ ነፋስ ወደ ኋላ እንዲሄድ በማድረግ ባሕሩን ደረቅ መሬት አደረገው። በዚህ መንገድ ውሃው ተከፈለ። 22 እስራኤላውያን በባሕሩ መካከል ገብተው በደረቅ መሬት ዐለፉ። ውሃው በቀኛቸውና በግራቸውና በኩል ግድግዳ ሆነላቸው። 23 ተከታትለዋቸው መጡ። እነርሱ፣ የፈርዖን ፈረሶች ሠረገሎችና ፈረሰኞች ሁሉ እስራኤላውያኑ ተከትለው በባሕሩ መካከል ገቡ። 24 ላይ እግዚአብሔር በእሳቱና በደመናው ዐምድ ውስጥ የግብፃውያንን ሰራዊት ወደ ታች ተመለከተ። በግብፃውያን መካከልም ሽብር እንዲፈጠር አደረገ። 25 የሠረገሎቻቸው መንኯራኵሮች ተቆላለፉ፤ ፈረሰኞችም ለመንቀሳቀስ እጅግ ተቸገሩ። ስለዚህ ግብፃውያኑ፣ እግዚአብሔር እኛን እየወጋላቸው ነውና፣ ከእስራኤል እንሽሽ” አሉ። 26 ሙሴን፣ “ውሃው በግብፃውያኑ፣ በሠረገሎቻቸውና በፈረሰኞቻቸው ላይ ተመልሶ እንዲመጣባቸው እጅህን በባሕሩ ላይ ዘርጋ” አለው። 27 እጁን በባሕሩ ላይ ዘረጋ፤ ንጋት ላይም ባሕሩ ወደ ተለመደ ስፍራው ተመለሰ። ግብፃውያኑ ከባሕሩ ሸሹ፤ እግዚአብሔር ግን ወደ ባሕሩ መካከል አስገባቸው። 28 ውሃው ተመስሎ በመምጣት የፈረዖንን ሠረገሎች፣ ፈረሰኞችን ሠረገሎቹን ተከትለው ወደ ባሕሩ የገቡትን ጠቅላላ ሰራዊቱን ሸፈናቸው። አንድም ሳይሰምጥ የቀረ አልነበረም። 29 ግን በባሕሩ መካከል በደረቅ መሬት ላይ ተራምደው ሄዱ። ውሃው በቀኛቸውም በግራቸውም በኩል ለእነርሱ ግድግዳ ሆናላቸዋል። 30 እግዚአብሔር በዚያ ቀን እስራኤላውያንን ከግብፃውያን እጅ ታደጋቸው፤ እስራኤላውያኑም የግብፃውያኑን ሬሳ በባሕሩ ዳር አዩ። 31 እግዚአብሔር በግብፃውያኑ ላይ የገለጠውን ታላቅ ኀይል ሲያዩ፣ ሕዝቡ እግዚአብሔርን አከበሩ፣ በእግዚአብሔርና በአገልጋዩ በሙሴም ታመኑ።



Exodus 14:1

• በሚግዶልና በባሕር መካከል፥ በበኣልዛፎንም

እነዚህ በምስራቃዊው ግብጽ ላይ ያሉ ከተሞች ናቸው

• ፈርዖንም ስለ እስራኤል ልጆች፦ በምድር ይቅበዘበዛሉ፥ ምድረ በዳም ዘጋቻቸው፥ ይላል

ይህ ቀጥተኛ ንግግር ቀጥታ ባልሆነ ሲጻፍ፦ “ንጉሡ ፈርዖን የእስራኤል ህዝብ በበረሓ ተዘግተው ወይም መንገድ አጥተው በአገሪቱ ዙሪያ የሚንከራተቱ ይመስለኛ” ብሎ አሰበ።

• ምድረ በዳም ዘጋቻቸው

ምድረ በዳው እስራኤላውያንን እንደጠለፋቸውና በአንድ ቤት ዘግቶ እንዳስቀመጣቸው አድርጎ ፈርዖን ይናገራል። ነገር ግን ሀሳቡ “እስራኤላውያን በምድረ በዳ መንገድ አጥተው” ማለት ነው።

Exodus 14:4

አጠቃላይ ምልከታ፦ እግዚአብሔር(ያህዌ) ሙሴ ወዴት መሄድ እንዳለበትና እግዚአብሔር (ያህዌ) ምን ሊያደርግ እንዳለ አመራር ሲሰጥ እናያለን። • እኔ የፈርዖንን ልብ አጸናለሁ

የፈርዖን ልብ የተባለው ራሱ ፈርዖን ማለት ነው። ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም ወይም እምብ አለ ማለት ነው። (ወካይ ወይም ተለዋጭ ዘይቤ ተመልከት)። በዚህኛ ክፍል የፈርዖንን ልብ ያደነደነው ወይም ፈርዖን እንዳይሰማ ያደረገው እግዚአብሔር እንደሆነ ነው። (ዘጸአት 9፡12 ተመልከት)

• እርሱም ያባርራቸዋል

በሌላ አገላለጽ፦ ፈርዖን እስራኤላውያንን ያብርራቸዋል ማለት ነው

• ክብር አገኛለሁ

ሰዎች እኔን ያከብሩኛል

• ግብፃውያንም እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ

በዚያን ጊዜ እኔ እግዚአብሔር እውነተኛ አምላክ እንደ ሆንኩ ግብጻውያን ያውቃሉ

• እነርሱም እንዲሁ አደረጉ

እስራኤላውያን እንደ ተነገራቸው አደረጉ ወይም እስራኤላውያን እግዚአብሔር እንደ ነገራቸው ፈጸሙ

• ለግብፅ ንጉሥ

ለግብጽ ንጉስ ፈርዖን

• ሕዝቡም እንደ ኮበለሉ

እስራኤላውያን እንዳመለጡ

• የፈርዖንና የባሪያዎቹም ልብ በሕዝቡ ላይ ተለወጠና

ፈርዖንና አገልጋዮቹ/መኳንንቱ/ ሀሳባቸውን ቀይረው ወይም ለውጠው

• እንዳይገዛልን እስራኤልን የለቀቅነው ምን አድርገናል?

ፈርዖንና መኳንንቱ ይህን ጥያቄ የጠየቁት የሞኝነት ተግባር እንደፈጸሙ ስላሰቡ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ይህ የሠራነው ነገር ምንድን ነው? እስራኤላውያንን እንዲሄዱ ፈቅደን አገልጋዮችን ማጣታችን አይደለምን? (አጋናኝ ጥያቄ የመተርግም ዘዴ ተመልከት)

Exodus 14:6

• ስድስት መቶ የተመረጡ ሰረገሎችን . . . ወሰደ

ስድስት መቶ (600) ምርጥ ሠረገሎችን . . . አሰለፈ

• እግዚአብሔር . . . የፈርዖንን ልብ አጸና

የፈርዖን ልብ የተባለው ራሱ ፈርዖን ማለት ነው። ፈርዖን ለመስማት አልፈለገም ወይም እምብ አለ ማለት ነው። (ወካይ ወይም ተለዋጭ ዘይቤ ተመልከት)። በዚህኛ ክፍል የፈርዖንን ልብ ያደነደነው ወይም ፈርዖን እንዳይሰማ ያደረገው እግዚአብሔር እንደሆነ ነው። (ዘጸአት 9፡12 ተመልከት)

• በኣልዛፎን . . . ፊሀሒሮት

በግብጽ ምስራቃዊው ክፍል የሚገኙ ከተሞች ነበሩ (ስሞችን የመተርጎም ዘዴ ተመልከት)

Exodus 14:10

• ፈርዖንም በቀረበ ጊዜ

በዚህ ክፍል “ፈርዖን” የተባለው መላውን የፈርዖን ሠራዊት የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ንጉሡ “ፈርዖንና ሠራዊቱ እየቀረቡ መምጣታቸውን”

• በግብፅ መቃብር ስላልኖረ በምድረ በዳ እንሞት ዘንድ አወጣኸንን?

እስራኤላውያን ይህንን ጥያቄ የጠየቁት እንዳይሞቱ ከመፍራታቸው እና ከመደንገጣቸው የተነሳ ነው። ይህን አጋናኝ ጥያቄ በመደበኛ ዐረፍተ ነገር ሲንተረጉም፦ በግብጽ ምድር በቂ የመቃብር ቦታ አለ፤ ለመቀበር ወይም መቃብር ፍለጋ እዚህ ምድረ በዳ መምጣት አልነበረብንም።

• ከግብፅ ታወጣን ዘንድ ይህ ያደረግህብን ምንድር ነው?

እስራኤላውያን ይህን ጥያቄ ሙሴን የጠየቁት በምድረ በዳ እንድሞቱ በማምጣቱ ለመገሰጽ ወይም ለመተቸት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ እኛን ከግብጽ አውጥተኸን እንዲህ ሊታሰቃየን አይገባህም ነበር።

• በግብፅ ሳለን ያልንህ ቃል ይህ አይደለምን?

ይህ አጋናኝ ጥያቄ የሚያሳየው ከዚህ በፊት በግብጽ እያሉ ለእርሱ የነገሩትን ለማስታወስ ወይም አትኩሮት ለመስጠት ነበር። አማራጭ ትርጉም፦ ይህ ሁሉ እንደሚሆን ገና ከዚያ ሳንወጣ ወይም በግብጽ ሳለን ነግረንህ አልነበረምን?

• ተወን፥ ለግብፃውያን እንገዛ ብለን

በሌላ አገላለጽ፦ “እባክህ ተወን ወይም ይቅርብን ለግብጻውያን ባርያዎች ሆነን እናገልግል” ብለን ነግረንህ ነበር

Exodus 14:13

• ሙሴም ለሕዝቡ

ሙሴ ለህዝቡ/ለእስራኤላውያን/ እንዲህ ብሎ መልስ ሰጣቸው

• ዛሬ ለእናንተ የሚያደርጋትን

እግዚአብሔር ዛሬ እናንተን እንዴት እንደምያድን/ለእናንተ እንዴት እንደሚሰራ/

• ዛሬ የምታዩአቸውን ግብፃውያንን ለዘላለም አታዩአቸውምና

ሙሴ እስራኤላውያንን በትህትና በማናገር እግዚአብሔር የግብጻውያንን ሰራዊት እንደሚደመስስ ይነግራቸዋል። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር ዛሬ የግብጻውያንን ሰራዊት ይገድላል። (በአይነኬ ዘይቤ የተነገረ)

Exodus 14:15

• ለምን ትጮኽብኛለህ?

ሙሴ እርዳታ ፍለጋ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበረና እግዚአብሔር ይህንን ጥያቄ ሙሴን ለማስገደድ ሲጠቀምበት እናያለን። ይህን አጋናኝ ጥያቄ በሁለት መንገድ በአጋናኝ ጥያቄ ወይም በመደበኛ ዐረፍተ ነገር መተርጎም ይቻላል። 1) “ሙሴ አንተ ወደ እኔ የምትጮኸው ለምንድን ነው?” 2) ሙሴ ከእንግዲህ ወዲህ ወደ እኔ አትጩህ ወይም ከእንግዲህ ወዲህ እኔን አትጥራ”

• ክፈለውም

ውሃውን ለሁለት ክፈለው ወይም ውሃው ለሁለት ይከፈላል

• እኔ የግብፃውያንን ልብ አጸናለሁ

“የግብጻውያንን ልብ” የተባለው ግብጻውያንን የሚመለከት ሲሆን “ገታራነታቸው ወይም እልከኝነታቸው” ልባቸው ጠንካራ እንደሆነ ተመስሎ ተነገረ። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ ግብጻውያን እንብተኞች ወይም እልከኞች አደርጋቸዋለሁ።

• በኋላቸውም ይገባሉ

ግብጻውያን እስራኤላውያንን ተከትለው ባህሩ ውስጥ ይገባሉ

Exodus 14:19

• በግብፃውያን ሰፈርና በእስራኤል ሰፈር መካከልም ገባ

በግብጻውያን ሠራዊት መካከል እና በእስራኤላውያን ሠራዊት መካከል

• ሌሊቱንም ሁሉ እርስ በእርሳቸው አልተቃረቡም

የግብጽ ሠራዊት ሌሊቱን ሙሉ ወደ እስራኤላውያን ሠራዊት መጠጋት አልቻለም ወይም የግብጽ ሠራዊትና የእስራኤል ሠራዊት አንዱ ሌላው ጋር መጠጋት አልቻሉም

Exodus 14:21

• የምሥራቅ ነፋስ አምጥቶ

ይህ ነፋስ ከምስራቅ በኩል ይነሳና ወደ ምዕራብ ይነፍሳል

• ምስራቅ

ፀሐይ የሚወጣበት አቅጣጫ

• ውኃውም ተከፈለ

በሌላ አገላለጽ፦ “እግዚአብሔር ውሃውን ከፈለው”

Exodus 14:23

• የግብፃውያንንም ሠራዊት አወከ

አንድ ሰው ከፍርሃት የተነሳ ሲታወክ በትክክል ማሰብ አይችልምና ከልክ በላይ ደነገጡ ወይም ፈሩ ወይም የሚሆኑትን አጡ ማለት ነው።

• የሰረገሎቹንም መንኮራኵር አሰረ

የሠረገላዎቻቸውን ብረት ጎማ ወይም መንኩራኮር ከመሬት ወይም ከጭቃ ጋር አጣበቀባቸው

Exodus 14:26

• እግዚአብሔርም ሙሴን፦ እጅህን በባሕሩ ላይ ዘርጋ፥ በግብፃውያን በሰረገሎቻቸውም በፈረሰኞቻቸውም

አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ ብሎ አዘዘው፦ “ውሃው በግብጻውያን ላይ፥ በሰረገላዎቻቸው ላይና በፈረሰኞቻቸው ላይ እንዲመለስ እጅህን በባህሩ ላይ ዘርጋ”

• ግብፃውያንም ከእርሱ ሸሹ

የእብራይስጡ ትርጉም ከባህሩ ሸሹ ሳይሆን ወደ ባህሩ ሮጡ የሚል ፍቺ አለው። ይህ ማለት ግብጻውያን ከውሃው መሸሽ ሲገባቸው እየዋጣቸው ወዳለው ውሃ ይሮጡ ነበር።

• እግዚአብሔርም ግብፃውያንን በባህሩ መካከል ጣላቸው

እግዚአብሔር (ያህዌ) ግብጻውያንን በባህሩ ውስጥ አሰጠማቸው

Exodus 14:29

• እስራኤልን

በተለያዩ ቦታዎች “እስራኤል” ተብሎ የተጠቀሰው “የእስራኤል ህዝብን” የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የእስራኤል ህዝብ ወይም እስራኤላውያን

• ከግብፃውያን እጅ አዳነ

“እጅ” የሚለው ቃል “ሀይልን” የሚመለከት ሲሆን እግዚአብሔር ከግብጻውያን ሀይል/ጥቃት/ጉልበት/ ማለት ይቻላል (ወካይ ዘይቤ ተመልከት)

• በባሕር ዳር አዩ

በባህሩ አጠገብ አዩ


Chapter 15

1 ጊዜ ሙሴና የእስራኤል ሕዝብ ይህን መዝሙር ለእግዚአብሔር እንዲህ እያሉ ዘመሩ፦ “በክብር ከፍ ከፍ ብሎአልና ለእግዚአብሔር እዘምራለሁ፤ ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባሕር ውስጥ ጥሎአል። 2 ብርታቴና ዝማሬዬ ነው፤ ድነቴም ሆኖልኛል። እርሱ አምላኬ ነው፣ አመሰግነዋለሁ፤ የአባቴ አምላክ ነው፣ ከፍ ከፍ አደርገዋለሁ። 3 ተዋጊ ነው፤ ስሙም እግዚአብሔር ነው። 4 ሠረገሎችና ሠራዊት በባሕር ውስጥ ጥሎአል። የፈርዖን ምርጥ መኮንኖች በቀይ ባሕር ውስጥ ሰመጡ። 5 ማዕበሎቹ ሽፈናቸው፤ እንደ ድንጋይ ወደ ጥልቆቹ ወረዱ። 6 እግዚአብሔር ሆይ፣ ቀኝ እጅህ ጠላትን ሰባበረ። 7 ላይ የተነሡትን በታላቅ ግርማ ገለበጥሃቸው። ቊጣህን ላክህ፤ እንደ ገለባም አርጎ በላቸው። 8 በአፍንጫህ እስትንፋስ ውሆች ተከመሩ፤ ፈሳሾች እንደ ክምር ቆሙ፤ የጥልቁ ውሃ በባሕሩ ውስጥ ረጋ። 9 ጠላት፣ ‘አሳድዳቸዋለሁ፣ እይዛቸዋለሁ፣ ምርኮም እካፈላለሁ፤ ፍላጎቴ በእነርሱ ርዳታ ያገኛል፤ ሰይፌን እመዝዛለሁ፤ እጄም ታጠፋቸዋለች’ አለ። 10 ግን በነፋስህ እፍ አልህ፣ ባሕሩም ሸፈናቸው፤ በኀይለኛ ውሆች ውስጥ እንደ ብረት ሰመጡ። 11 ሆይ፣ ክአማልክት መካከል እንደ አንተ ያለ ማን ነው? በቅድስና የከበረ፣ ተአምራትን በማድረግ በምስጋና ከፍ ያለ፣ እንደ አንተ ያለ ማን ነው? 12 እጅህን ዘረጋህ፤ ምድርም ዋጠቻቸው። 13 ፍቅርህ የታደግሃቸውን ሕዝብህን መራህ። በብርታትህ ወደ ቅዱስ ማደሪያህ መራሃቸው። 14 ይሰማሉ፣ ይንቀጠቀጣሉም፤ የፍልስጥኤምን ኗሪዎች ሽብር ይይዛቸዋል። 15 ጊዜ የኤዶም እለቆች ይደነግጣሉ፤ የሞዓብ መሪዎች ይርበደበዳሉ፤ የከነዓን ኗሪዎች ሁሉ ይቀልጣሉ። 16 ሆይ፣ ሕዝብህ እስከሚያልፉ፣ የታደግሃቸው ሕዝብህ ዐልፈው እስከሚሄዱ ድረስ፣ ሽብርና ድንጋቴ ይወድቅባቸዋል፤ ከክንድህ ብርታት የተነሣ፣ እንደ ድንጋይ የማይንቀሳቀሱ ይሆናሉ። 17 ሆይ፣ ማደሪያህ ባደረግኸው ስፍራ፣ ጌታችን ሆይ፣ እጆችህ በሠሩት መቅደስ፣ በርስትህ ተራራ ላይ ሕዝብህን ታመጣቸዋለህ፣ ትተክላቸዋለህም። 18 ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም ይነግሣል።” 19 ፈረሶች ከሠረገሎቹና ከፈረሰኞቹ ጋር ወደ ባሕሩ ውስጥ ሲገቡ፣ እግዚአብሔር የባሕሩን ውሀ መልሶ በላያቸው አመጣባቸው። እስራኤላውያን ግን በባሕሩ መካከል በደረቅ መሬት ሄዱ። 20 ይአሮን እኅት፣ ነቢይቱ ማርያም ከበሮ አነሣች፤ ሌሎቹ ሴቶችም በሙሉ ከበሮ ይዘው ከእርሷ ጋር እያሸበሸቡ ወጡ። 21 “ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባሕር ውስጥ ጥሎአል፤ በክብር ከፍ ከፍ ብሎአልና፣ ለእግዚአብሔር ዘመሩ” እያለች ዘመረችላቸው። 22 ሙሴ እስራኤላውያንን ከቀይ ባሕር እየመራቸው ወደ ሱር ምድረ በዳ ሄዱ። በምድረ በዳው ውስጥ ሦስት ቀን ሲጓዙ ውሀ አላገኙም። 23 ማራም ደረሱ፤ ነገር ግን እዚያ የሚገኘው ውሀ መራራ ስለ ነበረ ሊጠጡት አልቻሉም። ቦታውን ማራ ያሉት ከዚህ የተነሣ ነው። 24 ሕዝቡ፣ “ምን እንጠጣ?” ብለው በሙሴ ላይ አጕረመረሙ። 25 ወደ እግዚአብሔር ጮኸ፣ እግዚአብሔርም አንድ ዛፍ አሳየው። ሙሴም የዛፉን ዕንጨት ወደ ውሀው ውስጥ ጣለው፣ ውሀውም ጣፋጭ ሆነ። እግዚአብሔር ለሕዝቡ ሕግና ሥርዐት የሰጣቸውና የፈተናቸው በዚያ ስፍራ ነበር። 26 እንዲህ አለ፤ “የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ድምፅ በጥንቃቄ ብትሰሙ፥ ትክክለኛ የሆነውንም በፊቱ ብታደርጉ፣ ትእዛዛቱንም ብታስተውሉና ሕግጋቱን ሁሉ ብትጠብቁ፣ ግብፃውያን ላይ ካመጣኋቸው በሽታዎች አንዱንም በእናንተ ላይ አላመጣም፤ እኔ ፈዋሻችሁ እግዚአብሔር ነኝና።” 27 በኋላ ሕዝቡ ዐሥራ ሁለት ምንጮችና ሰባ የዘንባባ ዛፎች ወደ ነበሩበት ወደ ኤሊም መጡ። በዚያም በውሀው አጠገብ ሰፈሩ።



Exodus 15:1

አጠቃላይ ምልከታ፦ ይህ መዝሙር ወይም ምዕራፍ 15 በምዕራፍ 14፡26-28 በተከሰተው ከስተት ምክንያት የተዘመረ መዝሙር ነው • በክብር ከፍ ከፍ ብሎአልና

ይህ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ለድል አድራጊነቱ የተዘመረ መዝሙር ነው። በሌላ አገላለጽ፦ “እርሱ በግብጻውያን ላይ በታላቅ አሸናፊነት ተገለጸ” ወይም “እርሱ በግብጻውያን ታላቅ ድል ተጎናጸፈ”

• ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባሕር ጣለ

እግዚአብሔር በግብጻውያን ላይ ባህሩን መመለሱንና እነርሱን በባህር ማስጠሙን ሙሴ በሌላ አገላለጽ እግዚአብሔር በባህር ውስጥ እንደጣላቸው ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ “እርሱ በፈረሱና በፈረሰኛው ላይ ባህሩን መለሰባቸው” ወይም “እርሱ ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባህር አሰጠማቸው”

• ፈረሱንና ፈረሰኛውን

እስራኤላውያንን የሚያሳድዱ ብዙ ፈረሶችንና ፈረስ ጋላቢዎችን የሚገልጽ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ፈረሶችንና ፈረስ ጋላቢዎችን

Exodus 15:2

• እግዚአብሔር ጉልበቴ ነው (ወካይ ዘይቤ)

አማራጭ ትርጎሞች፦ 1) ሀይልን የሚሰጠኝ እግዚአብሔር ነው 2) እኔን የሚጠብቀኝ ወይም የሚከላከለኝ እግዚአብሔር ነው

• ዝማሬዬ እግዚአብሔር ነው (ወካይ ዘይቤ)

ሙሴ እግዚአብሔርን የዝማሬዬ ምንጭ ነው ወይም እግዚአብሔር እኔ የሚዘምርለት እርሱ ነው

• መድኃኒቴም ሆነልኝ (ወካይ ዘይቤ)

ሙሴ እግዚአብሔር መድሀኒቴ ብሎ ይጠራዋል ምክንያቱም እርሱ ከግብጻውያን እጅ አድኖአቸዋልና። አማራጭ ትርጉም፦ የሚያድነኝ እግዚአብሔር ነው

• እግዚአብሔር ተዋጊ ነው

ሙሴ እግዚአብሔርን ተዋጊ ብሎ ይጠራል ምክንያቱም እርሱ በሀይሉ ግብጻውያንን ተዋግቶ አሸንፏል። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር እንደ ብርቱ ተዋጊ ነው (ተለዋጭ ዘይቤ)

Exodus 15:4

• የፈርዖንን ሰረገሎች ሠራዊቱንም በባሕር ጣላቸው

ሙሴ ስለእግዚአብሔር ሲዘምር እግዚአብሔር ባህሩን በፈርዖን፥ ሰረገሎችና በሠራዊቱ ላይ መመለሱን በባህር ውስጥ እንደመጣል ተነግሯል። አማራጭ ትርጉም፦ እርሱ በፈርዖን ሰረገላዎችንና በሠራዊቱ ላይ ባህሩን መልሷል ወይም እርሱ የፈርዖን ሰረገላዎችንና ሠራዊቱን በባህር አስጥሟል

• ወደ ባሕር ጥልቀት እንደ ድንጋይ ሰጠሙ

ድንጋይ በባህር እስከ ውስጥ እንደሚሰጥም የጠላት ሠራዊት እስከ ባህሩ ጥልቅ ድረስ መስጠማቸውን ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ ድንጋይ በባህር ውስጥ እንደሚሰጥም እነርሱ በብሃር ውስጥ ሰጠሙ (ተነጻጻር ዘይቤ)

Exodus 15:6

• ቀኝህ በኃይል ከበረ

ሙሴ እግዚአብሔር እጅ እንዳለው አድርጎ ይናገራል፤ “ቀኝ እጅ” የእግዚአብሔርን ሀይል ወይም እግዚአብሔር በሀይሉ የሚሰራቸውን ነገሮች ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር ሀይልህ የከበረ ነው፤ እግዚአብሔር ሆይ አንተ በሀይልህ የምትሰራቸው ነገሮች ክቡር ናቸው (ወካይ ዘይቤ)።

• ቀኝህ ጠላቱን አደቀቀ

ሙሴ እግዚአብሔር እጅ እንዳለው አድርጎ ይናገራል፤ “ቀኝ እጅ” የእግዚአብሔርን ሀይል ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር ሆይ ሀይልህ ጠላቶችን አደቀቀ ወይም እግዚአብሔር ሆይ በሀይልህ ጠላቶችን አደቀቅህ

• የተነሡብህን አጠፋህ

በእግዚአብሔር ላይ ማመጽ በእግዚአብሔር ላይ እንደመነሳት ተቆጥሯል፤ አማራጭ ትርጉም፦ በአንተ ላይ ያመጹ ወይም ጠላቶችህን

• ቍጣህን ሰድደህ

የእግዚአብሔርን ቁጣ ሙሴ ሲገልጽ አንድ ነገር ለመሥራት እንደ ተላከ አገልጋይ አድርጎ ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ ቁጣህን አሳየህ ወይም አንተ እንደ ቁጣ ሥራህን ፈጸምክ

• እንደ ገለባም በላቸው

x

Exodus 15:9

• ነፍሴም ትጠግባቸዋለች

በሌላ አገላለጽ፦ እኔ ፍላጎቴን አሟላለሁ ወይም እኔ የፈለግሁትን ከእነርሱ እወስዳለሁ

• እጄም ታጠፋቸዋለች

ጠላቶች እስራኤላውያንን በእጃቸው ሀይል እንደሚያጠፉ ሲናገሩ እጃቸው እያጠፋቸው እንደሆነ አስመስለው ይናገራሉ። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ በእጄ አጠፋቸዋለሁ

• ነፋስህን አነፈስህ

ሙሴ እግዚአብሔር በአፉ ወይም በአፍንጫው ነፋሱን እንደነፈሰባቸው አድርጎ ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ ነፈሱ እንዲነፍስ አድርገሃል

• እንደ አረር ሰጠሙ

አረር ከባድ የብረት ዘር ሲሆን ነገሮች በውሃ ወይም በባህር ውስጥ እንድሰምጡ ሲፈለግ አረር ይጠቀማሉ። እዚህ ቦታ “አረር” የተጠቀሰበት ምክንያት ጠላቶች ምን ያህል ፈጥነው እንደ ጠፉ ለማሳየት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እንደ አረር ወይም ከባድ ብረት በሚናወጠው ውሃ ውስጥ ሰጥመው ቀሩ

• በአማልክት መካከል እንደ አንተ ያለ ማን ነው? (አጋናኝ ጥያቄ)

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የጠየቀው የእግዚአብሔርን ትልቅነት ለመግለጽ ሲፈልግ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር ሆይ፥ ከአማልክት መካከል አንተን የሚመስል ማን ነው?

• ድንቅንም የምታደርግ፥ እንደ አንተ ያለ ማን ነው? (አጋናኝ ጥያቄ)

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የጠየቀው የእግዚአብሔርን ትልቅነት ለመግለጽ ሲፈልግ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ታአምራትን የምታደርግ አንደ አንተ ያለ ማን ነው? ወይም ድንቅ ሥራዎችን የምትሰራ አንተን የሚመስል ማን ነው።

Exodus 15:12

• ቀኝህን ዘረጋህ

“ቀኝ እጅ” የእግዚአብሔርን ታላቅ ሀይል የሚገልጽ አባባል ሲሆን “በታላቅ ሀይልህ” የሚል ፍቺ አለው። “ዘረጋህ” የሚለው እግዚአብሔር እጅ እንዳለውና እጁን እንደዘረጋው አድርጎ ያሳያል። አማራጭ ትርጉም፦ በታላቅ ሀይልህ ይህን አደርግኸው

• ምድርም ዋጠቻቸው

ሙሴ በሰውኛ ዘይቤ ምድር አፍ እንዳላትና ነገሮችን መዋጥ ወይም መብላት እንደምትችል አድርጎ ያቀርባል። አማራጭ ትርጉም፦ ምድር በላቻቸው ወይም አጠፋቻቸው

Exodus 15:14

• ተንቀጠቀጡም

ይህ በፍርሃት ምክንያት መንቀጥቀጣቸውን የሚገልጽ ነው።

• በፍልስጥኤም የሚኖሩትን ምጥ ያዛቸው

ፍልስጥኤማውያን ወይም በፍልስጥኤም የሚኖሩ ሰዎች ተሸበሩ/ታወኩ/

• በከነዓን የሚኖሩ ሁሉ ቀለጡ

ሰዎች ከፍርሃት የተነሳ መድከማቸውን ሙሴ እንደ ቀለጡ አድርጎ ያሳያል። በሌላ አገላለጽ፦ የከነዓን ሕዝብ ወኔ ከዳቸው ወይም ድፍረት አጡ

Exodus 15:16

አያያዥ ዐረፍተ ነገር፦ ለሎች ህዝቦች የእግዚአብሔርን ህዝብ ሲያዩ ምን እንደሚሰማቸው ሙሴ በመዝሙር ይገልጻል። • ፍርሃትና ድንጋጤ ወደቀባቸው

አነዚህ ሁለቱ ቃላት የሚያሳዩት በእነርሱ ላይ ፍርሃት ሊመጣ እንደሆነ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “ፍርሃት በእነርሱ ላይ ይመጣል”

• በክንድህ ብርታት

የእግዚአብሔር ክንድ የእርሱን ትልቅ ሀይል የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ከሀይልህ ትልቅነት የተነሳ”

• እንደ ድንጋይ ዝም አሉ

አማራጭ ትርጉሞች፦ 1) እነርሱ እንደ ድንጋይ ዝም ይላሉ 2) እነርሱ እንደ ድንጋይ እንቅስቃሴ አልባ ይሆናሉ

Exodus 15:17

• አንተ ታስገባቸዋለህ

“አንተ ታስገባቸዋለህ” የሚለው በሌላ አገላለጽ፦ አንተ ህዝብህን ወደ ከነዓን ታመጣቸዋለህ ወይም ትወስዳቸዋለህ የሚል ነው።

• በርስትህ ተራራም ትተክላቸዋለህ

እግዚአብሔር የከነዓንን ምድር ለእስራኤላውያን ርስት አድርጎ መስጠቱን ሙሴ ተክል ከመትከል ጋር ሲያነጻጽር ይታያል። “የርስት ተራራ” የተባለው በከነዓን ምድር ያለው “የጽዮን ተራራ ነው”። እግዚአብሔር ምድርቱን እንደ ርስት አድርጎ ይሰጣቸዋል። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ እነርሱን በርስት ተራራቸው ታኖራቸዋለህ ወይም እነርሱ በርስት ተራራቸው ይኑሩ።

Exodus 15:19

• ማርያም . . . አሮን

ማርያም የሙሴና የአሮን ታላቅ እህት ነበረች።

• ከበሮ

ከሙዚቃ መሳሪያዎች አንዱ ሲሆን ከተለያዩ ቁሳቁሶች ይሰራል፤ ለምሳሌ ከብረት፥ ከእንጨትና ከቆዳ ወዘተ።

• በክብር ከፍ ከፍ ብሎአል

ይህ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ለድል አድራጊነቱ የተዘመረ መዝሙር ነው። በሌላ አገላለጽ፦ “እርሱ በግብጻውያን ላይ በታላቅ አሸናፊነት ተገለጸ ወይም እርሱ በግብጻውያን ታላቅ ድል ተጎናጸፈ (15፡1 ተመልከት)

• ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባሕር ጣለ

እግዚአብሔር በግብጻውያን ላይ ባህሩን መመለሱንና እነርሱን በባህር ማስጠሙን ሙሴ በሌላ አገላለጽ እግዚአብሔር በባህር ውስጥ እንደ አንድ ነገር እንደ ጣላቸው ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ እርሱ በፈረሱና በፈረሰኛው ላይ ባህሩን መለሰባቸው ወይም እርሱ ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባህር አሰጠማቸው (15፡1 ተመልከት)

Exodus 15:22

• ሙሴም እስራኤልን ከኤርትራ ባሕር አስጓዘ

“እስራኤል” የሚለው የእስራኤልን ህዝብ የሚወክል ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ሙሴ የእስራኤልን ህዝብ መራቸው

• ወደ ሱር ምድረ በዳ ወጡ . . . ወደ ማራም መጡ

እነዚህ ቦታዎች በትክክል የት ጋር እንደሆኑ በትክክል ማሳየት አይቻለም። ነገር ግን ቦታዎች ወይም መንደሮች ነበሩ፤ ምናልባት በከነዓን ምድር በደቡባዊ ምስራቅ የሚገኙ አከባቢዎች ሊሆኑ ይችላሉ።

Exodus 15:24

• በሙሴ ላይ አንጎራጎሩ

ህዝቡ በሙሴ ላይ ደስተኞች አለመሆናቸውን የሚገልጽ ነው፤ አማራጭ ትርጉም፦ በሙሴ ላይ አጉረመረሙ ወይም በሙሴ ላይ በቁጣ ተናገሩ

• የእግዚአብሔርን ቃል አጥብቀህ ብትሰማ

እግዚአብሔር ስለራሱ ድምጽ ይናገራል፤ ድምጹ እርሱን ይገልጻል ወይም ይወክላል። በሌላ አገላለጽ፦ ድምጼን ወይም እኔ የሚለውን (ወካይ ዘይቤ)

• በፊቱም የሚበጀውን ብታደርግ

“በፊቱ” የሚለው በእግዚአብሔር ፊት ሲሆን አንድ ሰው በእግዚአብሔር በዓይኑ ፊት ቆሞ አንድ ነገር እንደምፈጽም የሚናገር ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር የሚቀበለውን መልካም ነገር አድርጉ ወይም እግዚአብሔር የሚፈልገውን ነገር አድርጉ

Exodus 15:27

• ወደ ኤሊም መጡ

ውሃና መልካም አየር እንዲህም ትላልቅ ዛፎች ያሉበት ቦታ ነው።

• ሰባ የዘንባባ ዛፎች

“ዘንባባ” የተባለው በርግጥ ዘንባባ ሳይሆን ተምር ነው። ተምር በመልኩ ከዘንባባ ጋር ስለሚመሳሰል አማርኛው ትርጉም ዘንባባ ብሎታል። በሌላ አገላለጽ፦ ሰባ የተምር ዛፎች


Chapter 16

1 የእስራኤል ማኅበር አባላት ከኤሊም ተንሥተው፣ ከግብፅ ምድር ከወጡ በኋላ በሁለተኛው ወር ዐሥራ አምስተኛ ቀን በኤሊምና በሲና መካከል ወዳለው ወደ ሲን ምድረ በዳ መጡ። 2 በዳው ውስጥም ጠቅላላ የማኅበሩ አባላት በሙሴና በአሮን ላይ አጕረመረሙ። 3 ሙሴንና አሮንንም፣ “በሥጋ ምንቸቶች ዙሪያ ተቀምጠን እስክንጠግብ ምግብ በምንበላበት በግብፅ ምድር በእግዚአብሔር እጅ ምነው በሞትን ኖሮ፤ ከዚያ አውጥታችሁ ወደዚህ ምድረ በዳ ያመጣችሁን መላውን ማኅበራችንን በረኃብ ልትጨርሱ ነውና” አሏቸው። 4 ሙሴን እንዲህ አለው፤ “እንጀራ ከሰማይ አዘንብላችኋለሁ። በሕጌ የሚመሩ ወይም የማይመሩ መሆናቸውን እንድፈትናቸው፣ ሕዝቡ ይውጡና በየቀኑ ለአንድ ቀን የሚሆነውን ይሰብስቡ። 5 ቀን በየቀኑ ከሚሰበስቡት ዕጥፍ ይሰብስቡ፤ ያመጡትንም ያዘጋጁ።” 6 ከዚያም ሙሴና አሮን ለእስራኤል ሕዝቡ ሁሉ እንዲህ አሉ፤ “ከግብፅም ምድር ያወጣችሁ እግዚአብሔር እንደ ሆነ ማታ ታውቃላችሁ። 7 በእርሱ ላይ ያጕረመረማችሁትን ሰምቶአልና፣ የእግዚአብሔርንም ክብር ጠዋት ታያላችሁ። በእኛ ላይ ልታጕረመርሙ እኛ ለእናንተ ምንድን ነን?” 8 ደግሞ እንዲህ አለ፤ በእርሱ ላይ ያጕረመረማችሁትን ሰምቶታልና፣ እግዚአብሔር ማታ ሥጋ፣ ጠዋትም ምግብ እስክትጠግቡ ሲሰጣችሁ፣ ይህን ታውቁታላችሁ። አሮንና እኔ ምንድን ነን? የምታጕረመርሙት በእኛ ላይ ሳይሆን፣ በእግዚአብሔር ላይ ነው።” 9 ሙሴ አሮንን፣ “‘ጕርምርምታችሁን ሰምቶታልና ወደ እግዚአብሔር ፊት ቅረቡ’ በልህ ለእስራኤል ሕዝብ ማኅበር ሁሉ ተናገር’” አለው። 10 አሮን ለእስራኤል ሕዝብ ማኅበር ሁሉ እንደ ተናገረ፣ ወደ ምድረ በዳው ተመለከቱ፤ እነሆም፣ የእግዚአብሔር ክብር በደመናው ውስጥ ታየ። 11 እግዚአብሔርም ለሙሴ እንዲህ ብሎ ነገረው፤ 12 “የእስራኤልን ሕዝብ ጕርምርምታ ሰምቻለሁ። እንዲህ ብለህ ንገራቸው፤ ‘ማታ ሥጋ ትበላላችሁ፤ ጠዋት ደግሞ እንጀራ ትበሉና ትጠግባላችሁ። ከዚያም በኋላ እኔ አምላካችሁ እግዚአብሔር መሆኔን ታውቃላችሁ። 13 ላይ ድርጭቶች መጡና ሰፈሩን ሸፈኑት። በጠዋቱም የሰፈሩን ዙሪያ ጤዛ ተኝቶበታል። 14 ሲጠፋ፣ እንደ ዐመዳይ ያለ ስስ ቅርፊት በምድረ በዳው ላይ ታየ። 15 ሰዎች ሲያዩት፣ አንዳቸው ለአንዳቸው፣ “ምንድን ነው?” ተባባሉ። ምን እንደ ነበረ አላወቁም። ሙሴም እንዲህ አላቸው፤ “ይህ እንድትበሉት እግዚአብሔር የሰጣችሁ እንጀራ ነው። 16 እግዚአብሔር ይህን ትእዛዝ ሰጥቶአል፦ ‘ለመብላት የምትፈልጉትን መጠን በሕዝባችሁ ቊጥር ለያንዳንዱ ሰው አንድ ጎሞር ሰብስቡ። የምትሰበስቡት እንደዚህ ነው፦ በድንኳናችሁ ውስጥ ለሚኖር ለእያንዳንዱ ሰው ለመብላት የሚበቃውን ሰብስቡ።” 17 የተነገራቸውን አደረጉ። አንዳንዶች የበለጠ፣ አንዳንዶችም ያነሰ ሰበሰቡ። 18 በጎሞር መጠን ሲለኩት፣ ብዙ የሰበሰቡት የተረፈ አላገኙም፤ ትንሽ የሰበሰቡትም ያጡትናየጎደለባቸው አልነበረም። እያንዳንዱ ሰው የሰበሰበው ለፍላጎቱ የሚበቃውን ያህል ነበር። 19 “ማንም ሰው ለነገ ከእርሱ ምንም ማስተረፍ የለበትም” አላቸው። 20 ግን ሕዝቡ ሙሴን አልሰሙትም። አንዳንዶቻቸው ከሰበሰቡት እስከሚቀጥለው ጠዋት የተወሰነ አስቀሩ፤ ያስቀሩት ምግብ ግን ተላ፣ ሸተተም። ሙሴ ተቆጣቸው። 21 የሰበሰቡት ጠዋት ጠዋት ነበር። እያንዳንዱ ሰው ለቀኑ የሚበቃውን ሰበሰበ። ፀሐይ ስትሞቅ ቀለጠ። 22 ቀን ለያንዳንዱ ሰው ሁለት ሁለት ጎሞር እንጀራ አድርገው ዕጥፍ ሰበሰቡ። የማኅበረ ሰቡ አለቆችም በሙሉ መጥተው ለሙሴ ነገሩት። 23 “እግዚአብሔር ይህን ተናግሮአል፦ ‘ነገ ፍጹም ዕረፍት፣ ለእግዚአብሔር ክብር የተቀደሰ ሰንበት ነው። መጋገር የምትፈልጉትን ጋግሩ፤ መቀቀል የምትፈልጉትንም ቀቅሉ። ተርፎ የሚቀረውን ሁሉ እስከ ጠዋት ለራሳችሁ አስቀምጡት’” አላቸው። 24 የተረፈውን ሙሴ በነገራቸው መሠረት እስከ ጠዋት አቆዩት። አልሸተተም፤ ትልም አልነበረበትም። 25 እንዲህ አለ፤ “ዛሬ እግዚአብሔርን ለማክበር የተቀደሰ ሰንበት ነውና፣ ያስተረፋችሁትን ያን ምግብ ዛሬ ብሉት። ዛሬ ሜላ ላይ አታገኙትም። 26 ቀኖች ትሰበስቡታላችሁ፤ ሰባተኛው ቀን ግን የሰንበት ቀን ነው። በሰንበት ቀን መና የለም።” 27 ቀን አንዳንዶች መና ሊሰበስቡ ወጡ፣ ነገር ግን ምንም አላገኙም። 28 ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ትእዛዛቴንና ሕገጋቴን ለመጠበቅ እንቢ የምትሉት እስከ መቼ ነው? 29 በሉ፤ እግዚአብሔር ሰንበትን ሰጥቶአችኋል። ስለዚህ በስድስተኛው ቀን የሰጣችሁ ለሁለት ቀን የሚሆን እንጀራ ነው። ከእናንተ እያንዳንዱ በገዛ ስፍራው ይቆይ፤ በሰባተኛው ቀን ማንም ሰው ከስፍራው መውጣት የለበትም።” 30 በሰባተኛው ቀን ዐረፉ። 31 ምግቡን “መና” ብለው ጠሩት። ምግቡም እንደ ድንብላል ዘር ነጭ፣ ጣዕሙም በማር በስሱ እንደ ተጋገረ ቂጣ ነበረ። 32 ሙሴም፣ “እግዚአብሔር ያዘዘው ይህ ነው፦ ‘ከግብፅ ምድር ካወጣኋችሁ በኋላ በምድረ በዳ ያበላኋችሁን እንጀራ ልጆቻችሁ ማየት እንዲችሉ፣ አንድ ጎመር መና ለትውልዶቻችሁ ሁሉ ይቀመጥ” አለ። 33 አሮንን፣ “አንድ ማሰሮ ውሰድና አንድ ጎሞር መና አስቀምጥበት፤ ለትውልዶች ሁሉ ተጠብቆ እንዲቆይም በእግዚአብሔር ፊት አስቀምጠው” አለው። 34 ሙሴን ባዘዘው መሠረት፣ አሮን መናውን በምስክሩ ፊት አስቀመጠው። 35 ወደሚኖሩበት ምድር እስከሚመጡ ድረስ አርባ ዓመት መና በሉ። ወደ ከነዓን ምድር ድንበር እስከሚመጡ ድረስ የተመገቡት እርሱን ነው። 36 አንድ ጎመር የኢፍ አንድ ዐሥረኛ ነው።



Exodus 16:1

• ሲን ምድረ በዳ መጡ

“ሲን” የምድረ በዳው ስም ነው፤

• በሁለተኛው ወር ከወሩም በአሥራ አምስተኛው ቀን

በሁለተኛው ወር በአስራ አምስተኛ ቀን

• የእስራኤልም ልጆች ማኅበር ሁሉ

ይህ ግነታዊ ዘይቤ አገላለጽ ሲሆን “እስራኤላውያን ሁሉ” (ጠቅላይ እና ግነታዊ ዘይቤ)

• አንጎራጎሩ

አጉረመረሙ ወይም ተቆጡ ወይም ተናደዱ

• ምነው በሞትን

ይህ አገላለጽ አሁን ባለንበት ሁኔታ ውስጥ ከመጨናነቅ እዚያው ሞተን ቢሆን ይሻለን ነበር ብለው ተናገሩ። አማራጭ ትርጉም፦ ምነው በእግዚአብሔር (ያህዌ) እጅ ሞተን ባረፍነው ኖሮ ወይም ምነው በግብጽ ሳለን እግዚአብሔር በገደለን ኖሮ

• በእግዚአብሔር እጅ

“በእግዚአብሔር እጅ” የሚለው በአግዚአብሔር አሰራር ወይም እርምጃ የሚል ፍች አለው።

Exodus 16:4

• እነሆ ከሰማይ እንጀራን አዘንብላችኋለሁ

እግዚአብሔር ከሰማይ የሚልከውን ምግብ ከመዝነብ ጋር አነጻጽሯል። በሌላ አገላለጽ፦ ከሰማይ ምግብ እንደ ዝናብ እልክላችኋለህ /እሰጣችኋለህ/። “እንጀራ” የሚለው አንድ የተወሰነ የምግብ ዓይነት ይገልጻልና በአከባቢው የተለመደ ማንኛውንም የምግብ ዓይነት መጠቀም ይቻላል።

• በሕጌ ይሄዱ ወይም አይሄዱ እንደሆነ

ህጌን ይታዘዙ ወይም አይታዘዙ እንደሆነ ማለት ነው

• ህጌን

ትዕዛዜን ማለት ነው

Exodus 16:6

• በእኛም ላይ የምታንጎራጕሩ እኛ ምንድር ነን?

ሙሴና አሮን ይህን አጋናኝ ጥያቄ የጠየቁት ህዝቡ በእነርሱ ላይ ማጉረምረማቸው ስንፍና ወይም ሞኝነት እንደሆነ ለማሳየት ነው። በአጋናኝ ጥያቄ ወይም በመደበኛ ዐረፍተ ነገር መተርጎም ይችላል። አማራጭ ትርጉም፦ በእኛ ላይ የምታጒረመርሙት እኛ ምን ስለሆንን ነው? ወይም በእኛ ለማጉረምረም እኛ ብቁ ሰዎች አይደለንም

• እንጀራን እግዚአብሔር ይሰጣችኋል

ሙሴ “ምግብ” በማለት ፋንታ “እንጀራ ወይም ዳቦ” ይላል። ይህን ከሰማይ የሚሰጣቸውን ምግብ እንደ ሌሎቹ የምግብ ዓይነት ሁልጊዜ ይበሉታል።

• እኛም ምንድር ነን?

ሙሴ ይህን አጋናኝ ጥያቄ የጠየቃቸው እርሱና አሮን ህዝቡ የፈለጉትን ነገር ለመስጠት እንደማይችሉ ለመግለጽ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔና አሮን እናንተ የምትፈልጉን ነገር መስጠት አንችልም

• ማንጎራጎራችሁ በእግዚአብሔር ላይ ነው እንጂ በእኛ አይደለም

ህዝቡ ያጉረመረሙት የእግዚአብሔር አገልጋዮች በሆኑት በሙሴና በአሮን ላይ ነበር። በሙሴና በአሮን ላይ ማጉረምረም በተዘዋዋሪ በእግዚአብሔር ላይ እንደማጉረምረም ነው። አማራጭ ትርጉም፦ በእኛ ላይ ስታጒረመርሙ በእግዚአብሔር ላይ ማጒረምረማችሁ እንደሆነ እወቁ ወይም ማጉረምረማችሁ በእኛ ላይ ሳይሆን በርግጥ በእግዚአብሔር ላይ ነው

Exodus 16:9

• እነሆም

ይህ “እኔሆ” የሚለው ቃለ ህዝብ አንድ አስደናቂ ነገር እንዳየ ለማመልከት ወይም ትኩረት ለመሳብ ነው

• ማለዳም እንጀራን ትጠግባላችሁ

ሙሴ “ምግብ” በማለት ፋንታ “እንጀራ ወይም ዳቦ” ይላል። ይህን ከሰማይ የሚሰጣቸውን ምግብ እንደ ሌሎቹ የምግብ ዓይነት ሁልጊዜ ይበሉታል። አማራጭ ትርጉም፦ በማለዳ/ጧት/ የምትፈልጉትን ያህል ምግብ ትጠግባላችሁ

Exodus 16:13

• እንዲህም ሆነ

ይህ አገናኝ ሀረግ በታሪኩ ውስጥ ያለውን በጣም አስፈላጊውን ክፍል ለይቶ ያሳያል። በአንተ ቋንቋ እንዲህ ባለሁ ጉዳይ ላይ አገልግሎት የሚሰጥ ቃል ካለ መጠቀም ይችላል።

• ድርጭቶች

ትናንሸ የሆኑ የወፍ ዝሪያዎች ናቸው፤

• ደቃቅ ውርጭ

በጊዜው ለነበሩ ሰዎች “ውርጭ” ማለት ምን ማለት እንደሆነ ግልጽ ነው። በአማርኛ ውርጭ የሚለው ቃል ወደ ከባድ ብርድ ያደላል። ነገር ግን “ውርጭ” እንደ በረዶ የመጋገር ባህርይ ያለው ስለሆነ አመዳይ ወይም እንደ ቅርፍት የተጋገረ ነገር ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ዐመዳይ ይመስል ነበር ወይም አመዳይ የሚመስል የተጋገረ ነገር

• እግዚአብሔር የሰጣችሁ እንጀራ

ሙሴ “ምግብ” በማለት ፋንታ “እንጀራ ወይም ዳቦ” ይላል። ይህ ከሰማይ የሚሰጣቸው ምግብ እንደ ሌሎቹ የምግብ ዓይነቶች ሁልጊዜ ይበሉታል። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር የሰጣችሁ እንጀራ ወይም ዳቦ፥ ምግብ

Exodus 16:16

አገናኝ ዐረፍተ ነገር፦ ሙሴ እግዚአብሔር ስለምሰጠው ምግብ ለህዝቡ መናገሩን ቀጥሏል።• አንድ ጎሞር

አንድ ጎሞር ወደ ሁለት ሊትር ያህል ነው

Exodus 16:22

• እንዲህም ሆነ

ይህ ሀረግ በታሪኩ ውስጥ አዲስ ሀሳብ እየገባ ወይም እየጀመረ ስለመሆኑ ለማሳየት ነው። በቁጥር 22-23 ድረስ ባለው ክፍል በስድስተኛውና በሰባተኛ ቀን ህዝቡ መናውን እንዴት መጠቀም እንዳለባቸው ያሳያል። በአንተ ቋንቋ እንዲህ ያለ አገናኝ ሀረግ ካለ መጠቀም ጥሩ ነው።

• ነገ ዕረፍት ነው

ሥራ የማይሰራበትና እረፍት የሚደረግበት ቀን

Exodus 16:24

• አልሸተተም

በስብሶ መሽተት አልጀመረም

• የእግዚአብሔር ሰንበት ዛሬ ነውና ብሉት

ዛሬ ሰንበት ስለሆነ እግዚአብሔርን ለማከበር ብቻ ይውላል

Exodus 16:26

• ሰባተኛው ቀን ግን

ነገር ግን በቀን ሰባት

• መና

እግዚአብሔር በየቀኑ ወይም በየማለደኣ ለሰጣቸው ምግብ እስራኤላውያን የሰጡት ስም ነው።

• በእርሱ አይገኝም

ምንም ምግብ አይኖርም ወይም ምንም ነገር አይኖርም

Exodus 16:28

አጠቃላይ ዕይታ፦ እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል።• ትእዛዞቼንና ሕጎቼን ለመጠበቅ እስከ መቼ እንቢ ትላላችሁ?

እግዚአብሔር ይህን አጋናኝ ጥያቄ የጠየቀ ህዝቡ የእግዚአብሔርን ትዕዛዞች ስላልታዘዙ እነርሱን ለመተቸት ወይም ለመገሰጽ ነው። ይህን አጋናኝ ጥያቄ በመደበኛ ዐረፍተ ነገር ስንተረጉም፦ እናንተ እስራኤላውያን ትዕዛዞቼንና ህጎቼን ለመታዘዝ ፈቃደኛ አይደላችሁም

• እግዚአብሔር ሰንበትን እንደ ሰጣችሁ እዩ

እግዚአብሔር (ያህዌ) ሰንበትን የሰጣችሁ እንድታርፉ መሆኑን ልብ በሉ/አስተውል/

• በስድስተኛው ቀን የሁለት ቀን እንጀራ ሰጣችሁ

በስድስተኛው ቀን ለሁለት ቀን የሚበቃ ወይም የሚሆን ምግብ ስለምሰጣችሁ

Exodus 16:31

• እንደ ድንብላል ዘር ነጭ ነው

የድንብላል ዘር ከቅመም ዘሮች አንዱ ሲሆን ምግብ ጣዕም እንዲኖረው የሚያደርግ ነው

• እንደ ማር ቂጣ ነው

በጣም ቀጭን ቂጣ ወይም እንደ እንጀራ በቀጭኑ የተጋገረ ነገር ነው

• ጎሞር

አንድ ጎሞር ወደ ሁለት ሊትር ያህል ነው

Exodus 16:33

• ጎሞርም የኢፍ መስፈሪያ አሥረኛ ክፍል ነው

ጎሞርና ኢፍ ሁለቱም መለኪያዎች ናቸው። ኢፍ ወደ ሀያ ኪሎ ግራም ሲመዝን ጎሞር ሁለት ኪሎ ግራም ይመዝናል


Chapter 17

1 የእስራኤል ማኅበር የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመከተል ከሲን ምድረ በዳ ተነሡ፤ በራፊዲምም ሰፈሩ፤ ነገር ግን ሕዝቡ የሚጠጡት ውሀ አልነበረም። 2 ሕዝቡ ሙሴን ወቀሡት፤ “የምንጠጣው ውሀ ስጠን” ብለውም ተናገሩት። ሙሴም፣ “ለምን እኔን ትጣሉኛላችሁ? እግዚአብሔርንስ ለምን ትፈታተኑታላችሁ?” አላቸው። 3 ያ ሕዝቡ ውሀ በጣም ጠምቷቸው ስለ ነበር በሙሴ ላይ አጕረመረሙ። እንዲህም አሉት፤ “እኛንና ልጆቻችንን፣ ከብቶቻችንንም በውሀ ጥም ለመፍጀት ከግብፅ ለምን አወጣኸን?” 4 እነዚህን ሰዎች ምንድን ነው ማድረግ ያለብኝ? በድንጋይ ሊወግሩኝ ተዘጋጅተዋል” በማለት ወደ እግዚአብሔር ጮኸ። 5 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ከእስራኤል ሽማግሌዎች አንዳንዶችን፣ ወንዙን የመታህበትንም በትር ያዝና ከሕዝቡ ፊት ቀድመህ ሂድ። 6 ኮሬብ ባለው ዐለት ላይ እኔ ከፊትህ እቆማለሁ፤ ዐለቱንም ትመታዋለህ። ከእርሱም ሕዝቡ የሚጠቱት ውሀ ይወጣል።” ሙሴም በእስራኤል ሽማግሌዎች ፊት የታዘዘውን አደረገ። 7 ስላጕረመረሙና “እግዚአብሔር በመካከላችን አለ ወይስ የለም?” በማለት እግዚአብሔርን ስለ ተፈታተኑት ያን ስፍራ ማሳህና መሪባ ብሎ ጠራው። 8 መጥተው እስራኤልን ራፊዲም ላይ ወጉ። 9 ስለዚህም ሙሴ ኢያሱን፣ “ጥቂት ሰዎችን ምረጥና ውጣ፤ ከአማሌቃውያን ጋርም ተዋጋ። ነገ እኔ የእግዚአብሔን በትር ይዤ በኮረብታው ዐናት ላይ እቆማለሁ” አለው። 10 ሙሴ ባዘዘው መሠረት አማሌቃውያን ተዋጋቸው፤ ሙሴ፣ አሮንና ሖርም ወደ ኮረብታው ዐናት ወጡ። 11 እጁን ወደ ላይ ሲያነሣ፣ እስራኤላውያን ድል ያደርጉ ነበር፤ እጁን ሲያወርድ ግን አማሌቃውያን ለማሸነፍ ይጀምሩ ነበር። 12 የሙሴ እጆች እየደከሙ ሲሄዱ፣ አሮንና ሖር ድንጋይ ወስደው እንዲቀመጥበት ከእርሱ ሥር አስቀመጡለት። በዚያውም ጊዜ አሮንና ሖር አንዳቸው በአንድ ጎኑ፣ የቀረውም በሌላው ጎኑ በኩል በመሆን የሙሴን እጆች ወደ ላይ ደግፈው ያዙ። የሙሴ እጆችም ፀሐይ እስክትገባ ድረስ ጠንክረው ቆዩ። 13 ስለዚህም ኢያሱ አማሌቃውያንን በሰይፍ ድል አደረጋቸው። 14 እግዚአብሔር ሙሴን፣ “የአማሌቃውያንን መታሰቢያ ከሰማይ በታች ሙሉ በሙሉ ስለምደመስስ፣ ይህን በመጽሐፍ ጽፈህ ኢያሱ እየሰማ አንብበው” አለው። 15 ሙሴም መሠዊያ ሠርቶ፣ “እግዚአብሔር አርማዬ ነው” ብሎ ሰየመው። 16 “እጅ ወደ እግዚአብሔር ዙፋን ተነሥቶአልና፣ እግዚአብሔር በአማሌቃውያን ላይ ከትውልድ እስከ ትውልድ ጦርነት ያደርጋል” አለ።



Exodus 17:1

• ሲን ምድረ በዳ

“ሲን” የምድረ በዳው ስም ነው፤ (ዘጸአት 16፡1 ተመልከት)

• በራፊዲምም ሰፈሩ

በጉዞ ላይ ሰዎች የሚያርፉበት ወይም የሚቀመጡበት ሥፍራ ነው፤

• ለምን ትጣሉኛላችሁ? እግዚአብሔርንስ ለምን ትፈታተናላችሁ?

ሙሴ እነዚህን ጥያቄዎች የጠየቃቸው ህዝቡን ለመገሰጽ ወይም ለመኮነን ነው። ይህ አጋናኝ ጥያቄ በመደበኛ ዐረፍተ ነገር ምተርጎምም ይቻላል፤ ከእኔ ጋር ልትጣሉ አይገባችሁም፤ እግዚአብሔርንም (ያህዌን) ልትፈታተኑ አያስፈልጋችሁም

• እኛንና ልጆቻችንን ከብቶቻችንንም በጥማት ልትገድል ለምን ከግብፅ አወጣኽን?

እስራኤላውያን ይህንን እአጋናኝ ጥያቄ የጠየቁት በምድረ በዳ ልገድላቸው እንዳመጣቸው አድርገው ሙሴን ለመክሰስ ነው። ይህን አጋናኝ ጥያቄ በመደበኛ ዐረፍተ ነገር መተርጎምም ይቻላል፦ አንተ ከግብጽ ምድር ያወጣኸን እኛን፥ ልጆቻችንን እና ከብቶቻችንን በውሃ ጥም ለመፍጀት ወይም ለመግደል ነው

Exodus 17:4

• በሕዝቡ ፊት እለፍ

ከሕዝቡ ቀድም ብለህ ወደ ፊት ሂድ ወይም ከህዝቡ ፊት አልፈህ ሂድ

• ማሳህ . . . መሪባ ብሎ ጠራው

በምድረ በዳ ያለ ቦታ ሲሆን የስሙ ትርጉም “መፈታተን” ማለት ነው፤ “መሪባ” በምድረ በዳ ያለ ሥፍራ ሲሆን የስሙ ትርጉም “ማጉረምረም” ማለት ነው።

Exodus 17:8

• ራፊዲምም

በምድረ በዳ ያለ ሥፍራ ሲሆን ሰዎች በጉዞ ላይ ሲሆኑ የሚያርፉበት ወይም የሚቀመጡበት ሥፍራ ነው፤

• ኢያሱም . . . ከአማሌቅም ጋር ተዋጋ

ኢያሱ ራሱንና ለውጊያ የመረጣቸውን እስራኤላውያንን ወክሎ ቀርቧል። አማራጭ ትርጉም፦ ኢያሱና እርሱ የመረጣቸው ሰዎች አማሌቃውያንን ወጉት

• ሖር

የሙሴና የአሮን ጓደኛ

Exodus 17:11

• እስራኤል ድል ያደርግ ነበር . . . አማሌቅ ድል ያደርግ ነበር

እስራኤልና አማሌቅ ከሁለቱም ወገን ለውጊያ የተሰለፉ ሰዎችን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እስራኤላውያን ድል ያደርጉ ነበር . . . አማሌቃውያን ያሸንፉ ነበር

• የሙሴ እጆች ግን ከብደው ነበር

ፀሐፊው የሙሴ እጆች መድከማቸውን ለማሳየት ሲፈልግ እንደ ከበዱ አድርጎ ይገልጻል፤ በሌላ አገላለጽ፦ የሙሴ እጆች ደክመው ወይም ዝለው ነበር

• በሰይፍ ስለት አሸነፈ

በሰይፍ ተዋግቶ ድል አደረገ

Exodus 17:14

• የአማሌቅን ዝክር ከሰማይ በታች ጨርሼ እደመስሳለሁና

እግዚአብሔር የአማሌቅን መደምሰስ ሲገልጽ የአንድን ሰው የማሰብ አቅምን ከማጥፋት ጋር ሲያነጻጽር ይታያል። አንድ ሰው ወይም ቡድን ወይም ማህበረሰብ ፈጽሞ ሲጠፋ የምያስታውሳቸው ወይም መታሰቢያ ይጠፋል። በሌላ አገላለጽ፦ እኔ አማሌቃውያንን ፈጽሞ አጠፋለሁ ወይም እደመስሳለሁ (ተለዋጭ ዘይቤ)

• እጁን በእግዚአብሔር ዙፋን ላይ ስለጫነ

እጅ የማንሳት ልምምድ የሚታወቀው ሰዎች መሀላ ሲፈጽሙ ወይም ቃል ኪዳን ሲገቡ እጃቸውን ሲያነሱ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ምክንያቱም እጆች ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) ዙፋን ተዘርግተዋል ወይም ምክንያቱም ሙሴ እጁን ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) ስላነሳ

• በአማሌቅ

በአማሌቃውያን ላይ ወይም በአማሌቅ ሰዎች ላይ


Chapter 18

1 ካህን፣ የሙሴ ዐማት ዮቶር ለሙሴና ለሕዝቡ ለእስራኤላውያን እግዚአብሔር ያደረገውን ሁሉ ሰማ። እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከግብፅ ያወጣቸው መሆኑን ዮቶር ሰምቶ ነበር። 2 ሙሴ ወደ ቤት ከመለሳት በኋላ፣ የሙሴ ዐማት ዮቶር የሙሴን ሚስት ሲፓራን፣ 3 ምድር ባዕድ ነበርሁ” ሲል ጌርሳም ብሎ የጠራውንና ሌላውንም ልጅ ተቀብሏቸው ነበር። 4 “የአባቶቼ አምላክ ረድቶኛል፤ ከፈርዖንም ሰይፍ አድኖኛል” ብሎ ነበርና፣ የሌላው ልጁ ስም አልዓዛር ነው። 5 ዐማት ዮቶር ከሙሴ ልጆችና ከሚስቱ ጋር በምድረ በዳው ውስጥ በእግዚአብሔር ተራራ አጠገብ ሰፍሮ ወደ ነበረው ወደ ሙሴ መጣ። 6 ሙሴን፣ “እኔ ዐማትህ፣ ዮቶር ከሚስትህና ከልጆችህ ጋር ወደ አንተ እየመጣሁ ነው” አለው። 7 ዐማቱን ሊቀበለው ወጣ፤ ሰገደ፤ ሳመውም። ስለ እያንዳንዳቸው ደኅንነት ተጠያይቀው ወደ ድንኳኑ ውስጥ ገቡ። 8 ሙሴም እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ሲል በፈርዖንና በግብፃውያን ላይ ያደረገውን በሙሉ፣ በመንገድም በእነርሱ ላይ የደረሰባቸውን ችግር ሁሉና እግዚአብሔር እንዴት እንደታደጋቸው ለዐማቱ ነገረው። 9 ዮቶር እስራኤላውያንን ከግብፃውያን እጅ በመታደግ እግዚአብሔር ባደረገው መልካም ነገር ሁሉ ተደሰተ። 10 እንዲህ አለ፤ “ከግብፃውያን እጅና ከፈርዖን እጅ አድኖአችኋል፤ ሕዝቡንም ከግብፃውያን እጅ ታድጎአቸዋልና እግዚአብሔር ይመስገን። 11 እግዚአብሔር ከአማልክት ሁሉ ታላቅ እንደ ሆነ አሁን ዐውቃለሁ፤ ምክንያቱም ግብፃውያን እስራኤላውያንን በትዕቢት ይዘዋቸው በነበረ ጊዜ፣ እግዚአብሔር ሕዝቡን ታድጎአል።” 12 ዐማት ዮቶር የሚቃጠል መሥዋዕቶችን ለእግዚአብሔር አቀረበ። አሮንና የእስራኤል አለቆች ሁሉ ከሙሴ ዐማት ጋር በእግዚአብሔር ለመብላት መጡ። 13 በሚቀጥለው ቀን ሙሉ ሕዝቡን ሊዳኝ ተቀመጠ። ሕዝቡ ከጠዋት እስከ ማታ ድረስ በእርሱ ዙሪያ ቆሙ። 14 የሙሴ ዐማት ሙሴ ለሕዝቡ ያደረገውን ሁሉ ተመልክቶ፣ “ምን እያደረግህ ነው? ብቻህን ለምን ትቀመጣለህ? ሰዎችስ ሁሉ ከጧት እስከ ማታ ድረስ ለምን በአንተ ዙሪያ ይቆማሉ?” አለው። 15 ዐማቱን እንዲህ አለው፤ “ሰዎቹ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለመጠየቅ ወደ እኔ ይመጣሉ። 16 ሲኖራቸው፣ ወደ እኔ ይመጡና በመካከላቸው ላለው ችግር ውሳኔ እሰጣለሁ፤ የእግዚአብሔርን ሕገጋትና ሥርዐትም አስተምራቸዋለሁ።” 17 ዐማቱም ሙሴን መልሶ እንዲህ አለው፤ “የምታደርገው ተገቢ አይደለም። 18 ዐብረውህ ያሉ ሰዎች በእውነት ራሳችሁን ታደክማላችሁ። ይህ ለአንተ ከባድ ሸክም ነው። ይህን ተግባር ብቻህን ማከናወን አትችልም። 19 ስማኝ። ምክር እሰጥሃለሁ፤ እግዚአብሔርም ከአንተ ጋር ይሆናል፤ ምክንያቱም አንተ በእግዚአብሔር ፊት የሕዝቡ ወኪል ነህ፤ አቤቱታቸውንም ወደ እግዚአብሔር ታቀርባለህ። 20 ሥርዐታትና ሕገጋት ልታስተምራቸው፣ የሚሄዱበትን መንገድና የሚሠሩትን ሥራም ልታሳያቸው ይገባል። 21 እግዚአብሔርን የሚፈሩ ችሎታቸውን፣ ኢፍትሓዊ ጥቅምን የሚጠሉ የእውነት ሰዎችንከሕዝቡ ሁሉ ምረጥ። ዕነርሱን መሪዎች እንዲሆኑ በሕዝቡ ላይ ሸለቆች፣ መቶ አለቆች፣ ዐምሳ አለቆችና ዐሥር አለቆች አድርገህ ሹማቸው። 22 ጉዳዮችን ሁሉ በሚመለከት ሕዝቡን የሚዳኙት እነርሱ ይሆናሉ፤ ከባድ ከባድ ጉዳዮችን ግን ወደ አንተ ያቀርባሉ። አነስተኛ ጉዳዮችን ሁሉ በሚመለከት፣ እነርሱ ራሳቸው ውሳኔ ሊሰጡባቸው ይችላሉ። በዚህ መንገድ ሥራው ለአንተ ይቀልልሃል፤ እነርሱም ሸክሙን ከአንተ ጋር ይሸከማሉ። 23 ይህን ብታደርግና እግዚአብሔርም እንደዚሁ እንድታደርግ ቢያዝዝህ፣ በርትተህ መሥራት ትችላለህ፤ መላው ሕዝብም ረክቶ ወደ ቤት መሄድ ይችላል።” 24 የዐማቱን ምክር በመስማት የነገረውን ሁሉ አደረገ። 25 ሙሴ ከእስራኤል ሁሉ ችሎታ ያላቸውን ሰዎች መረጠ፤ ሸለቆች፣ መቶ አለቆች፣ ዐምሳ አለቆችና ዐሥር አለቆች አድርጎም የሕዝቡ መሪዎች እንዲሆኑ ሾማቸው። 26 በቀላላል ጉዳዮች ሕዝቡን ይዳኙ ነበር። ከበባድ ጉዳዮችን ለሙሴ አቀረቡ፤ ትንንሽ ጉዳዮችን ሁሉ ግን እነርሱ ለራሳቸው ብያኔ ሰጡባቸው። 27 በኋላ ሙሴ ዐማቱን አሰናበተው፤ ዮቶርም ወደ ገዛ ምድሩ ተመልሶ ሄደ።



Exodus 18:1

• የሙሴ አማት

የሙሴ የሚስቱ አባት

• የሙሴን ሚስት ሲፓራን ሁለቱንም ልጆቿን ወሰደ

ይህ ሀረግ ሁለት ፍችዎችን ይዟል፦ 1) ዮቶር ሲፖራንና ሁለቱን ልጆቹን ወደ ሙሴ አመጣቸው 2) ዮቶር ሲፖራንና ሁለቱን ልጆች ወደ ቤት መልሶአቸው ነበር

• ዮቶር መልሶአት የነበረውን

ይህ አባባል ቀደም ብሎ ሙሴ የሰራውን ወይም ዮቶር ያደረገውን የሚያሳይ ነው። በሌላ አገላለጽ፦ ሙሴ ሚስቱን ወደ አማቾቹ ቤት ከላከ በኋላ

• ጌርሳም

የሙሴና የሲፖራ ልጅ ሲሆን የስሙ ትርጉም እንግዳ ወይም መጻተኛ ማለት ነው

• አልዓዛር

የሙሴና የሲፖራ ልጅ ሲሆን የስሙ ትርጉም እግዚአብሔር ረዳቴ ማለት ነው

• ከፈርዖንም ሰይፍ አዳነኝ

በፈርዖን ወይም በፈርዖን ሠራዊት ከመገደል መትረፉን ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ በፈርዖን ወይም በፈርዖን ሠራዊት ከመገደል/ከመሞት/ አዳነኝ።

Exodus 18:5

• በምድረ በዳ ወደ ሰፈረ

እርሱ ከእስራኤላውያን ጋር ወደ ሰፈረበት ወደ ምድረ በዳ

Exodus 18:7

• ሰገደም፥ ሳመውም

ሰዎች ታላቅ አክብሮትና ትህትናን እየሰጡ ስለመሆናቸው የሚያሳዩት እንደ ባህሉ በመሳምና እጅ በመንሳት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ራሱን ዝቅ አድርጎ እጅ በመንሣት ሳመው

• ስለ እስራኤል ያደረገውን ሁሉ

እግዚአብሔር ለእስራኤል ሲል ያደረጋቸውን ነገሮች ሁሉ

• በመንገድም ያገኛቸውን ድካም ሁሉ

በመንገድ ላይ ስላጋጠማቸው መከራ ሁሉ ወይም የደረሰባቸውን ፈተና ሁሉ

Exodus 18:9

• ከግብፃውያንና ከፈርዖን እጅ ያዳናችሁ

“እጅ” አንድ ሰው አንድን ነገር ለማድረግ የሚያስችል ሀይል እንዳለው የሚገልጽ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ከሀያላን ግብጻውያንና ከሀያሉ ፈርዖን ያተረፋችሁ/ያስመለጣችሁ/ያዳናችሁ/ (ወካይ ዘይቤ)

Exodus 18:13

• ይህ በሕዝቡ የምታደርገው ምንድር ነው?

ዮቶር ይህንን አጋናኝ ጥያቄ የጠየቀው ሙሴ የሚያደርገው ነገር ጥሩ ወይም ትክክል እንዳለሆነ ለማሳየት ነው። በትርጉም ውስጥ አጋናኝ ጥያቄውን እንዳለ ማምጣጥ ይቻላል ወይም ወደ መደበኛ ዐርረፍተ ነገር መቀየር ይቻላል። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ በህዝቡ ላይ ይህን ሁሉ ነገር ማድረግ አልነበረብህም ወይም ለህዝቡ የምታደርገው ይህ ሁሉ ነገር ምንድን ነው?

• አንተ ብቻህን ስለ ምን ተቀምጠሃል?

“ተቀምጠሃል” የሚለው ቃል ወካይ ዘይቤ ሲሆን “ለፍርድ” ወይም “ለህዝቡ ፍርድ ለመስጠት” መቀመጡን ለማሳየት ነው። ዳኞች የሰዎችን ጉዳይ ለመስማት እና ለመዳኘት መቀመጣቸውን ሲገልጽ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ ብቻህን ትፈርዳለህ” ወይም “ህዝቡ ላይ እየፈረድክ ያለኸው አንተ ብቻ ነህ (ወካይ ዘይቤ)

• ሕዝቡ ሁሉ ከጥዋት ጀምሮ እስከ ማታ ድረስ በዙሪያህ ቆመው ሳሉ አንተ ብቻህን ስለ ምን ተቀምጠሃል?

ዮቶር ይህን አጋናኝ ጥያቄ የጠየቀው ሙሴ ብዙ ሥራ ብቻውን እየሰራ መሆኑን አጽንዖት ሰጥቶ ለመናገር ፈልጎ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ይህ ሁሉ ሰው ከጧት እስከ ማታ ድረስ በአንተ በዙሪያ ቆሞ ሳለ አንተ ብቻህን በፍርድ ወንበር ላይ ለምን ትቀመጣለህ? ወይም ይህ ሁሉ ሰው ከጧት እስከ ማታ ድረስ በአንተ ዙሪያ ቆሞ ሳለ አንተ ብቻህን ለፍርድ መቀመጥ አይገባህም

Exodus 18:15

• ሕዝቡ እግዚአብሔርን ለመጠየቅ

ሕዝቡ /ሰዎች/ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ ወይም ለመፈለግ/ለመረዳት/

Exodus 18:17

• ይህ ነገር ይከብድብሃል

ዮቶር ሙሴ የሚሰራው ሥራ ከባድ መሆኑ ለማመልከት አንድን ነገር ከመሸከም ጋር ያነጻጽራል። አማራጭ ትርጉም፦ ሥራው ከአቅምህ በላይ ነው (ተለዋጭ ዘይቤ)

• አንተ ከአንተም ጋር ያለው ሕዝብ ትደክማላችሁ

አንተ ራስህንም ሆነ ሕዝቡን በከንቱ ታደክማለህ

• አሁንም እመክርሃለሁ

“ምክር እሰጥሃለሁ” ወይም “አቅጣጫ እጠቅምሃለሁ”

• እግዚአብሔርም ከአንተ ጋር ይሆናል

“ከአንተ ጋር ይሆናል” የሚለው የእግዚአብሔር እርዳታ ወይም እግዚአብሔር እንደምረዳው ለመግለጽ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር ይረዳሃል ወይም እግዚአብሔር ለሥራው ጥበብ ይሰጥሃል

• ነገራቸውንም ወደ እግዚአብሔር አድርስ

ዮቶር ሲናገር ሙሴ የህዝቡን ጥያቄ ወይም አቤቱታ ወደ እግዚአብሔር ለማድረስ ይዞ እንደምመጣ አድርጎ ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ ጥያቄአችውን ለእግዚአብሔር ተናገር/አሳውቅ/

• የሚሄዱበትን መንገድ የሚያደርጉትንም ሥራ ሁሉ አሳያቸው

ህዝቡ እንዴት መኖር እንዳለባቸውና ምን ማድረግ እንደሚገባቸውም መናገር ወይም ማሳየት አለብህ እንደማለት ነው

Exodus 18:21

አያያዥ ዐረፍተ ነገር፦ ዮቶር ንግግሩን ይቀጥላል •አንተም . . . ሰዎች ምረጥ

በተጨማሪ/ነገር ግን/ አንተ . . . ሰዎችን ምረጥ

• የሺህ አለቆችን፥ የመቶ አለቆችን፥ የአምሳ አለቆችን፥ የአሥርም አለቆችን

ይህ አባባል ሁለት ዓይነት ፍቺዎች ይኖሩታል፦ 1) እነዚህ ቁጥሮች በእያንዳንዱ ቡድን ውስጥ ያሉትን የሰዎች ቁጥር ወይም ብዛት አመልካች ናቸው፤ አማራጭ ትርጉም፦ “1000 ሰው ያለበት ቡድን፥ 100 ሰው ያለበት ቡድን፥ 50 ሰው ያለበት ቡድን እና 10 ሰው ያለበት ቡድን”፤ 2) እነዚህ ቁጥሮች በትክክል የሚታዩ ቁጥሮች ሳይሆኑ ምሳሌያዊ ናቸው፤ አማራጭ ትርጉም፦ “በጣም ትንሽ ሰው ቡድን መሪ፤ የትንሽ ሰው ቡድን መሪ፤ የብዙ ሰው ቡድን መሪ፤ በጣም ብዙ ሰው ቡድን መሪ”

• ሹምላቸው

በህዝቡ ላይ መፍረድ እንዲችሉ ሰይማቸው ወይም ሥልጣን ስጣቸው

• ታናሹንም ነገር ሁሉ እነርሱ ይፍረዱ

ከባድ ያልሆኑ ወይም ቀላል በሆኑ ነገሮች ላይ እነርሱ ይፍረዱ/ይወስኑ/

• አውራውን ነገር ሁሉ ወደ አንተ ያምጡት (ተለዋጭ ዘይቤ)

አስቸጋሪ የሆነውን ጉዳይ ሁሉ ለአንተ እንዲያቀርቡ /ለአንተ እንድነግሩ/ አድርግ ወይም ከአቅማቸው በላይ የሆነውን ከባድ ጉዳይ ወደ አንተ ያምጡት

• ከአንተ ጋር ሸክሙን ይሸከማሉ

ዮቶር ይህንን ሲናገር እነዚህ ሰዎች ከሙሴ ጋር አብረው አንድን ነገር ለመሸከምና እርሱን ለመርዳት የመጡ አስመሎ ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ ሥራውን በመሥራት ስለሚያግዙህ ሥራው ቀላል ይሆናል ወይም ከአንተ ጋር አብረው ስለሚሰሩ ሥራው ቀላል ይሆንልሃል

• ለአንተም ይቀልልልሃል

የሥራ ክብደቱ ለአንተ ቀላል ይሆናል ወይም የሥራ ጫና ይቀንስልሃል

Exodus 18:24

• ከእስራኤል ሁሉ አዋቂዎችን መረጠ

ፀሐፊው የሚናገረው አንድን ነገር ለማድረግ የሚያስችል አቅም ወይም ችሎታ እንጂ ዕውቀት አይደለም። ከእስራኤላውያን መካከል ችሎታ ያላቸውን ሰዎች መረጠ ወይም ከእስራኤላውያን መካከል ነገር የመለየት ችሎታ ያላቸውን መረጠ

• የሺህ አለቆችን፥ የመቶ አለቆችን፥ የአምሳ አለቆችን፥ የአሥርም አለቆችን

ኡህ አባባል ሁለት ዓይነት ፍቺዎች ይኖሩታል፦ 1) እነዚህ ቁጥሮች በእያንዳንዱ ቡድን ውስጥ ያሉትን የሰዎች ቁጥር አመልካች ናቸው፤ አማራጭ ትርጉም፦ “1000 ሰው ያለበት ቡድን፥ 100 ሰው ይለበት ቡድን፥ 50 ሰው ያለበት ቡድን እና 10 ሰው ያለበት ቡድን”፤ 2) እነዚህ ቁጥሮች በትክክል የሚታዩ ቁጥሮች ሳይሆኑ ምሳሌያዊ ናቸው፤ አማራጭ ትርጉም፦ “በጣም ትንሽ ሰው ቡድን መሪ፤ የትንሽ ሰው ቡድን መሪ፤ የብዙ ሰው ቡድን መሪ፤ በጣም ብዙ ሰው ቡድን መሪ”

• በሕዝቡም ላይ ሁልጊዜ ፈረዱ

እነርሱ ሁልጊዜ የሕዝብ ዳኞች ሆነው አገለገሉ/ያገለግሉ ነበር/

• የከበደባቸውንም ነገር ወደ ሙሴ አመጡ

አስቸጋሪ የሆኑትን ጉዳዮች ብቻ ወደ ሙሴ ያቀርቡ ነበር ወይም አስቸጋሪ በሆኑ ነገሮች ላይ ሙሴ እንዲፈርድ ወደ እርሱ ያመጡ ነበር

• ታናሹን ነገር ሁሉ ግን እነርሱ ፈረዱ

ቀላል በሆነው ነገር ላይ እነርሱ ራሳቸው ይወስኑ ነበር

• የህጉ መገለጥ

በዚህ ምዕራፍ የተገለጹ ነገሮች የሙሴን ህግ እንዲቀበሉ ህዝቡን የሚያዘጋጅ ነበር። ህጉን ለመቀበል ህዝቡ ህጉ የሚጠይቀውን እያንዳንዱን ነገር ለመማርና ለማድረግ ራሳቸውን ማዘጋጀት አለባቸው። የዚህ ምዕራፍ ክስተት ለእስራኤል አስፈላጊና ዋናው አካል ነበር።


Chapter 19

1 ወር፣ እስራኤላውያን ከግብፅ ምድር በወጡበት በዚያው ቀን ወደ ሲና ምድረ በዳ መጡ። 2 ከራፊዲም ከተነሡ በኋላ፣ ወደ ሲና ምድረ በዳ መጥተው በምድረ በዳው ውስጥ ከተራራው ፊት ለፊት ሰፈሩ። 3 ወደ እግዚአብሔር ወጣ። እግዚአብሔርም ከተራራው ጠርቶት እንዲህ አለው፤ 4 “ለያዕቆብ ቤት፣ ለእስራኤል ሕዝብ እንደዚህ ብለህ ተናገር፦ በግብፃውያን ላይ ምን እንዳደረግሁ ፣ እናንተንም በርግም ክንፎች እንዴት እንደ ተከከምኋችሁና ወደ ራሴ እንዴት እንዳመጣኋችሁ አይታችኋል። 5 ቃሌን በታዛዥነት ብትሰሙና ኪዳኔንም ብትጠብቁ፣ ከሕዝብ ሁሉ መካከል የእኔ ርስት ትሆናላችሁ፤ ምድር ሁሉ የእኔ ነውና። 6 እናንተ ለእኔ የካህናት መንግሕትና ቅዱስ ሕዝብ ትሆናላችሁ። ለእስራኤላውያን የምትነግራቸው ቃሎች እነዚህ ናቸው። 7 መጣ፤ የሕዝቡንም ሽማግሌዎች ጠርቶ እግዚአብሔር ያዘዘውን እነዚህን ቃሎች ሁሉ በፊታቸው ተናገረ። 8 ሁሉ በአንድነት፣ “እግዚአብሔር የተናገረውን ሁሉ እናደርጋለን” በማለት መልስ ሰጡ። ሙሴ ሕዝቡ የተናገሩትን ወደ እግዚአብሔር ለማቅረብ መጣ። 9 ሙሴን፤ “እኔ ከአንተ ጋር ስነጋገር፣ መስማት እንዲችሉና አንተንም ሁልጊዜ እንዲያምኑህ፣ ወደ አንተ በከባድ ደመና እመጣለሁ” አለው። ሙሴም ሕዝቡ የተናገሯቸውን ቃሎች ለእግዚአብሔር ነገረው። 10 ሙሴን፣ “ወደ ሕዝቡ ሂድ። ዛሬና ነገ ለእኔ ቀድሳቸው፤ ልብሳቸውንም እንዲያጥቡ አድርግ። 11 ቀንም ይዘጋጁ፤ በሦስተኛው ቀን እኔ እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ እወርዳለሁና። 12 ዙሪያ ሁሉ ለሕዝቡ ወሰን አብጅና ለሕዝቡ እንዲህ በላቸው፤ ‘ወደ ተራራው እንዳትወጡ ወይም የተራራውን ግርጌ ጫፍ እንዳትነኩ ተጠንቀቁ። ተራራውን የነካ ይሞታል።’ 13 ዐይነቱን ሰው ማንም አይንካው። እንዲያውም የነካው በድንጋይ ይወገራል ወይም በቀስታ ይወጋል። ሰውም ሆነ እንስሳ ይሞታል። መለከቱ የማያቋርጥ ድምፅ ሲያሰማ፣ ሕዝቡ ወደ ተራራው መውጣት ይችላሉ” አለው። 14 ሙሴም ከተራራው ወደ ሕዝቡ ወረደ። ሕዝቡን ለእግዚአብሔር ቀደሳቸው፤ ልብሳቸውንም አጠቡ። 15 “በሦስተኛው ቀን ተዘጋጁ፤ ወደ ሚስቶቻችሁም አትጠጉ” አላቸው። 16 ቀን ጠዋት ላይ ነጏድጓድና የመብረቅ ብልጭታ፣ ከባድ ደመና እና ጉሉሕ የመለከት ድምፅ በተራራው ላይ ነበሩ። በሰፈሩ ውስጥ የነበሩ ሰዎች ሁሉ ተንቀጠቀጡ። 17 ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር እንዲገናኙ ሕዝቡን ከሰፈር አወጣቸው፤ በተራራው ግርጌም ቆሙ። 18 እግዚአብሔር በእሳትና በጢስ ወርዶበት ስለ ነበረ፣ የሲና ተራራ ሙሉ በሙሉ በጢስ ተሸፈነ። ጢሱ እንደ ምድጃ ጢስ ይወጣ ነበር፤ ጠቅላላ ተራራውም በኀይል ተናወጠ። 19 ድምፅ እየጨመረና እየጎላ ሲሄድ፣ ሙሴ ተናገረ፤ እግዚአብሔርም በድምፅ መለሰለት። 20 እግዚአብሔር በሲና ተራራ ጫፍ ላይ ወርዶ፣ ሙሴን ወደ ተራራው ጫፍ እንዲወጣ ጠራው። ሙሴም ወጣ። 21 ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ለማየት ዐልፈው ወደ እኔ እንድይመጡ፣ ሂድና ሕዝቡን አስጠንቅቃቸው፤ አለዚያ ብዙዎች ይሞታሉ። 22 ወደ እኔ የሚቀርቡ ካህናትም ራሳቸውን ይቀድሱ፤ እንዳላጠፋቸውም ለእኔ መምጣት ራሳቸውን ያዘጋጁ።” 23 እግዚአብሔርን፣ “ሕዝቡ ወደ ተራራው መውጣት አይችሉም፤ ምክንያቱም ‘በተራራው ዙሪያ ወሰን አብጅና ለእግዚአብሔር ቀድሰው’ ብለህ አዝዘኸናል” አለው። 24 ሙሴን፣ “ከተራራው ወርደህ ሂድና አሮንን ክአንተ ጋር ይዘኸው ና፤ ካህናቱና ሕዝቡ ግን ወሰን ዐልፈው ወደ እኔ እንዲመጡ አትፍቀድላቸው፤ አለዚያ አጠፋቸዋለሁ” አለው። 25 ስለዚህ ሙሴ ወደ ሕዝቡ ሄዶ ይህንኑ ነገራቸው።



Exodus 19:1

• በሦስተኛውም ወር የእስራኤል ልጆች ከግብፅ ምድር ከወጡ በኋላ በዚያ ቀን . . .

እስራኤላውይ ወደ ሲና ምድረ በዳ የደረሱት በሶስተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን ልክ ከግብጽ በወጡበት በዚያች ቀን ነበር። ይህ ማለት ከግብጽ የወጡበትና ወደ ምድረ በዳ የደረሱበት ቀን ተመሳሳይ ነበር ማለአት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ "በሶስተኛው ወር እስራኤላውያን ግብፅን ለቀው በወጡበት በዚያችው በተመሳሳይ ዕለት . . .

• ራፊድም

ይህ ሥፍራ የሚገኘው በሲና ምድረ በዳ ጫፍ አከባቢ እስራኤላውያን የሰፈሩበት ሥፍራ ነው (ዘጸአት 17፡1 ተመልከት)

Exodus 19:3

• የያቆብ ቤት

“የያዕቆብ ቤት” የሚለው የያዕቆብን ቤተሰብ እና ትውልዱን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የያዕቆብ ተወላጆች ለሆኑት

• ለያቆብ ቤት . . . ለእስራኤልም ልጆች

“የእስራኤል ልጆች” የሚለው ሀረግ የሚገልጸው “የያዕቆብ ቤት” የሚለውን የሚያብራራ ነው።

• በንስርም ክንፍ እንደ ተሸከምኋችሁ

እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ያደረገውን ጥበቃና ጥንቃቄ ሲገልጽ እርሱ ንስር እንደ ሆነና እነርሱን በክንፉ እንደ ተሸከማቸው አድርጎ ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ ንስር ጫጩቶችዋን በክንፎችዋ እንደምትሸከም እኔም እናንተን እንዴት እንደተሸከምኳችሁ

• ቃሌን በእውነት ብትሰሙ

“ቃሌን ብትሰሙ” የሚለው እንዲሁ መስማት ብቻ ሳይሆን መታዘዝንም ይጨምራል። በሌላ አገላለጽ፦ ቃሌን ብትሰሙና ለእኔም ብትታዘዙ

• ኪዳኔንም ብትጠብቁ

ቃል ኪዳኔ የምጠይቃችሁን ነገር ብትፈጽሙ

• ርስት ትሆኑልኛላችሁ

የእኔ ርስት ወይም ሀብት ትሆናላችሁ

• የካህናት መንግስት . . . ትሆኑልኛላችሁ (ተለዋጭ ዘይቤ)

እግዚአብሔር ህዝቡ ካህናት እንደሆኑ ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ የመንግስት ህዝብ የሆናችሁ ለእኔ እንደ ካህናት ናችሁ ወይም የመንግስት ህዝብ የሆናችሁ እናንተ ለእኔ ካህናት የሚሰሩትን የምትሰሩ ናችሁ

Exodus 19:7

• ይህን ቃል ሁሉ በፊታቸው ተናገረ

ይህ ሀረግ የሚያሳየን ሙሴ ለህዝቡ ሲናገር ቃሉን ለፊታቸው እንደተናገረ አድርጎ ያቀርባል። አማራጭ ትርጉም፦ እነዚህን ቃሎች ሁለ ለእነርሱ ተናገረ

• እግዚአብሔር ያዘዘውን

እግዚአብሔር ለእርሱ የሰጠውን ትዕዛዝ

• ሙሴም የሕዝቡን ቃል ወደ እግዚአብሔር አደረሰ

ሙሴ እነርሱ ያሉትን መልሶ ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) ወሰደ ወይም ለእግዚአብሔር ሪፖርት አደረገ

• የሕዝቡን ቃል

“የህዝቡ ቃል” ህዝቡ የተናገሩትን የሚገልጽ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ህዝቡ ያሉትን ወይም የተናገሩትን

Exodus 19:10

• ዛሬና ነገም ቀድሳቸው

የዚህ ሀረግ ትርጉም:- ራሳቸውን ቅዱስ እንዲያደርጉ ወይም እንዲለዩ ለህዝቡ ንገራቸው

• ለሦስተኛው ቀን ይዘጋጁ

ይህ ትዕዛዛዊ ሀረግ ሲሆን በሌላ አገላለጽ፦ ህዝቡ ራሳቸውን እንዲያዘጋጁ ትዕዛዝ ተሰጣቸው

Exodus 19:12

አጠቃላይ ዕይታ፦ እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል። •ለሕዝቡ በዙሪያው ወሰን አድርግላቸው

በህዝቡ ዙሪያ ደንበር ወይም ገደብ አድርግ ወይም ህዝቡ እንዳያልፉ ድንበር ወይም ገደብ አበጅላቸው

• ተራራውንም የነካ ፈጽሞ ይሞታል

ማንም ሰው ተራራውን ቢነካ በርግጥ ይሞታል ወይም ተራራውን የሚነካ ማንም ቢሆን ግደሉት

• የሚነካው ሁሉ ይወገራል ወይም በፍላጻ ይወጋል

ተራራውን የሚነካ በድንጋይ ተወግሮ ወይም በቀስት ተወግቶ ይሙት

• ሳያቋርጥ የመለከት ድምፅ ሲነፋ

ከፍ ባለ ድምፅ ወይም ለረጅም ጊዜ ጥሩንባ በተነፋ ጊዜ

Exodus 19:14

• ወደ ሴቶቻችሁ አትቅረቡ

ይህ በትህትና የተገለጸው ወደ ሌላ ሴት ሳይሆን ወደ ሚስቶቻቸው እንዳይቀርቡ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ከሚስቶቻችሁ ጋር አትተኙ ወይም ከሚስቶቻችሁ ጋር ግብረ ሥጋ ግንኙነት አታድርጉ

Exodus 19:16

• እግዚአብሔር . . . ስለ ወረደበት

እግዚኢአብሔር ከተራራው ስለመጣ ወይም ስለወረደ

• እንደ እቶን ጢስ ያለ ጢስ ይወጣ ነበር

ጪሱ ከትልቅ የእሳት ምድጃ ወይም ከትልቅ የእሳት ቃጠሎ እንደሚወጣ ጪስ ነበር

• የእቶን ጢስ

በጣም ትልቅና የሚያቃጥል የእሳት ምድጃ

Exodus 19:19

• የቀንደ መለከቱም ድምፅ እጅግ በበረታና በጸና ጊዜ

የእምቢልታው ወይም የጥሩንባው ድምጽ እየበረታ ወይም እያየለ በመጣ ጊዜ

• እግዚአብሔርም በድምፅ መለሰለት (ወካይ ዘይቤ)

እዚህ ቦታ “ድምጽ” እግዚአብሔር የሚያሰማውን ድምጽ የሚመለከት ነው። የዚህ ሀረግ ፍቺው 1) እንደ መብረቅ እግዚአብሔር በትልቅ ድምጽ ተናግሯል 2) መብረቅ ድምጽ እንዲያወጣ በማድረግ 3) እግዚአብሔር ራሱ በከፍተኛ ድምጽ ተናገረ

• ሙሴን ወደ ተራራው ራስ ጠራው

ሙሴ ተራራው ላይ እንዲወጣ ጠየቀው/አዘዘው/

• ዳርቻውን እንዳያልፉ

የተወሰነውን ክልል ወይም ድንበር አልፈው እንዳይመጡ

Exodus 19:23

• ውረድ

ከተራራው ላይ ውረድ/ሂድ/

• አይተላለፉ

የተወሰነውን ክልል ወይም ድንበር አልፈው እንዳይመጡ


Chapter 20

1 እነዚህን ቃሎች እንዲህ በማለት ተናገረ፦ 2 ከግብፅ ምድር፣ ከባርነት ምድር ያወጣሁህ አምላክህ እግዚአብሔር ነኝ። 3 ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይኑሩህ። 4 በላይ በሰማይ ያለውን፣ ወይም በታች በምድር ያለውን፣ ከምድርም በታች በውሀ ውስጥ ያለውን የማንኛውንም ነገር የተቀረጸ ምስልና ሥዕል ለራስህ ጣዖት አታብጅ። 5 አትስገድላቸው፤ አታምልካቸውም፤ እኔ እግዚአብሔር አምላክህ ቀናተኛ አምላክ ነኝና። የሚጠሉኝን ሦስትና አራት ትውልድ በልጆች ላይ ቅጣት በማምጣት የአባቶችን ኀጢአት እቀጣለሁ። 6 በሚወዱኝና ትእዛዛቴን በሚጠብቁት በሺዎች ላይ ግን የኪዳን ታማኝነት አሳያለሁ። 7 የአምላክህን የእግዚአብሔርን ስም በከንቱ አታንሣ፤ ስሜን በከንቱ የሚያነሣውን በደል ዐልባ አላደርገውምና። 8 እንድትቀድሰው፣ የሰንበትን ቀን ዐስብ። 9 ቀን ሥራ፤ ተግባርህንም ሁሉ አከናውን። 10 ቀን ለእኔ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ሰንበት ነው። በሰንበት ቀን አንተም ወንድ ልጅህም፣ ሴት ልጅህም፣ ወንድ አገልጋይህም፣ ሴት አገልጋይህም፣ እንስሳትህም፣ በግቢህ ያለ እንግዳም ሥራ አትሠሩም። 11 እግዚአብሔር ሰማያትን፣ ምድርንና ባሕርን፣ በእነርሱ ውስጥ ያለውንም ሁሉ በስድስት ቀን ፈጥሬ በሰባተኛው ቀን ዐርፌአለሁና። ስለዚህ እኔ እግዚአብሔር የሰንበትን ቀን ባረክሁት፤ ለራሴም ቀደስሁት። 12 እኔ እግዚአብሔር አምላክህ በምሰጥህ ምድር ብዙ ጊዜ እንድትቆይ፣ አባትህንና እናትህን አክብር። 13 አትግደል። 14 አታመንዝር። 15 አትስረቅ። 16 በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር። 17 የባልንጀራህን ቤት አትመኝ፤ የባልንጀራህን ሚስት፣ ወንድ አገልጋዩን፣ ሴት አገልጋዩን፣ በሬውን፣ አህያውን፣ ወይም የባልንጀራህ የሆነውን ማንኛውንም ነገር አትመኝ።” 18 ሰዎች ሁሉ ነጎድጓዱንና መብረቁን አዩ፤ የመለከቱን ድምፅም ሰሙ፤ የሚጨሰውንም ተራራ ተመለከቱ። ሕዝቡ ይህን ሲያዩ፣ ተንቀጠቀጡ፤ ርቀውም ቆሙ። 19 ሙሴን፣ “አንተ ተናገረን፤ እኛም እንሰማሃለን፤ ነገር ግን እግዚአብሔር እንዲናገረን አታድርግ፤ አለዚያ እንሞታለን” አሉት። 20 ሙሴም ሕዝቡን፣ “አትፍሩ፤ ፈሪሀ እግዚአብሔር በእናንተ ዘንድ እንዲገኝና ኀጢአት እንዳትሠሩ ሊፈትናችሁ እግዚአብሔር መጥቶአልና” አላቸው። 21 ስለዚህ ሕዝቡ ርቀው ቆሙ፤ ሙሴም እግዚአብሔር ወዳለበት ወደ ጨለማው ተጠጋ። 22 ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ለእስራኤላውያን የምትነግራቸው ይህ ነው፦ ‘እኔ ከሰማይ ከእናንተ ጋር እንደ ተነጋገርሁ እናንተ ራሳችሁ አይታችኋል። 23 በቀር ሌሎች አማልክትን፣ የብር ወይም የወርቅ አማልክትን ለራሳችሁ አታብጁ። 24 የጭቃ መሠዊያ ሥራልኝ፣ በእርሱም ላይ የሚቃጠሉትን መሥዋዕቶችህን፣ የኅብረት መሥዋዕቶችህን፣ በጎችህንና በሬዎችህን ሠዋበት። ስሜ እንዲከበር በማደርግበት ስፍራ ሁሉ፣ ወዳንተ እመጣለሁ፤ እባርክሃለሁም። 25 መሠዊያ የምትሠራልኝ ከሆነ፣ በተጠረበ በድንጋይ አትሥራው፤ ለመጥረብ ስትል መሣሪያህን በላዩ ካሳረፍህበት ታረክሰዋለህና። 26 ሆነህ እንዳትጋለጥ፣ በመሠዊያዬ ላይ በደረጃ አትውጣ።”



Exodus 20:1

• ከባርነት ቤት

በባርነት የነበራችሁበት ቦታ

• ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ

ከእኔ በስተቀር ሌሎችን አማልክት አታምልክ

Exodus 20:4

• የማናቸውንም ምሳሌ፥ የተቀረጸውንም ምስል ለአንተ አታድርግ

የማንኛውንም ዐይነት ምስል ተጠቅመህ ለራስህ ጣዖት አድርገህ አትሥራ

• አትስገድላቸው፥ አታምልካቸውምም

ማንኛውንም ጣዖት አታምልክ ለእርሱም እጅ ነስተህ አትስገድለት

• እኔ . . . ቀናተኛ አምላክ ነኝ

እግዚአብሔር ህዝቡ እርሱን ብቻ እንዲያመልኩት ይፈልጋል

• የአባቶችን ኃጢያት በልጆች ላይ የማመጣ

እግዚአብሔር ስለአባቶቻቸው ሀጢአት ልጆችን ወይም የሚቀጥለውን ትውልድ የሚቀጣ መሆኑን ይገልጻል

• እስከ ሦስተኛና እስከ አራተኛ ትውልድ ድረስ

እስከ የልጅ ልጅ ድረስ

• እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ ምሕረትን የማደርግ

“ምህረት” የሚለው ቃል በዕብራይስጡ እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ታማኝ መሆኑን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔን ለሚወዱ ቃል ኪዳኔን እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ የሚጠብቅ ታማኝ አምላክ ነኝ

• እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ

“ሺህ” የሚለው ቃል በወካይ ዘይቤ የተጠቀሰ ሲሆን የብዙ አመታትን ቁጥር የሚገልጽ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እስከ ዘላለም ድረስ

Exodus 20:7

• የአምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ

የአምላክህን ስም በከንቱ ወይም በግድየለሽነት ወይም በንቀት አታንሣ ወይም አትጠቀም

• ከበደል አያነጻውም

ይህ ድርብ አሉታዊ አገላለጽ እግዚአብሔር ሳይቀጣ እንደማያልፍ ለማመልከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ በደለኛውን በርግጥ እቀጣለሁ

Exodus 20:8

• ተግባርህንም ሁሉ አድርግ

በየቀኑ የምታደርጋቸውን ተግባራት በየዕለቱ ፈጽም

• በደጆችህም ውስጥ ያለ እንግዳ

በአይሁዶች በቀድሞ ልምድ ከተሞች ዙሪያቸው የታጠረና ሰዎች እንድገቡና እንድወጡ በርም ነበራቸው። አማራጭ ትርጉም፦ በአገርህ ውስጥ የሚኖሩ መጻተኞችም ወይም በአጥርህ ውስጥ የሚኖሩ የሌሎች አገሮች ሰዎች

• የሰንበትን ቀን ባርኮታል

ሁለት አማራጭ ትርጉሞች፦ 1) እግዚአብሔር የሰንበት ቀን መልካም ነገር እንዲያመጣ/እንዲያፈራ/ አድርጎታል 2) እግዚአብሔር የሰንበት ቀን መልካም ነው ብሏል

• የሰንበትን ቀን ቀድሶታል

የሰንበትን ቀን ለራሱ ለይቶታል

Exodus 20:12

• አታመንዝር

ከሚስት ወይም ከባል ጋር ካልሆነ በቀር ከማንም ጋር ግብረ ሥጋ ግንኙነት አታድርግ

Exodus 20:15

• በሐሰት አትመስክር

በማንም ሰው ላይ በሐሰት አትመስክር ወይም ስለአንድ ሰው በውሸት አትናገር

• አትመኝ

አንድን ነገር ለማግኘት ከልክ በላይ አትፈልግ ወይም ለራሴ ይሁንልኝ ብለህ አትመኝ

Exodus 20:18

• የቀንደ መለከቱን ድምፅ

ከቀንድ የተሰራ ድምጽ ማውጫ። ይህን ድምጽ ማውጫ መሳሪያ ለማያውቁ በስዕል ማሳየት ይቻላል።

• ተራራውንም ሲጤስ

ከተራራው ላይ ጭስ ሲወጣ ወይም በተራራው ቃጠሎ ምክንያት ጭስ ሲወጣ

• ተርበደበዱ

በፍርሃት ተንቀጠቀጠቀጡ

• ርቀውም ቆሙ

“ራቅ ብለው ቆሙ” ወይም “በርቀትም ቆሙ”

• ኃጢያትንም እንዳትሠሩ እርሱን መፍራት በልባችሁ ይሆን ዘንድ

እግዚአብሔርን በመፍራት ወይም በማክበር ኃጢአት ከመሥራት ተቆጥባችሁ እንድትኖሩ ነው”

• ሙሴም . . . ወደ ጨለማው ቀረበ

ሙሴ . . . ጥቅጥቅ ወደ ሆነው ደመና ተጠጋ/ሄደ/

Exodus 20:22

• ለእስራኤል ልጆች እንዲህ በል

ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ንገራቸው

• እኔ ከሰማይ እንደ ተናገርኋችሁ እናንተ አይታችኋል

ከሰማይ ሆኜ እንደ ተናገርኋችሁ እናንተ ራሳችሁ አይታችኋል

• በአጠገቤ ምንም አታድርጉ

እኔን ትታችሁ ሌሎችን አማልክት በጣኦት መልክ አትሥሩ

• የብር አማልክት የወርቅም አማልክት ለእናንተ አታድርጉ

ከብርና ከወርቅ የተሰሩ ጣኦታት ወይም ከብርና ከወርቅ የተሰሩ አማልክት

Exodus 20:24

• የጭቃ መሰዊያ ሥራልኝ

ከአፈር፥ ከድንጋይ ወይም ከሸክላ የተሰራ መሰዊያ

• ስሜን በማሳስብበት ስፍራ ሁሉ

“ስም” የእግዚአብሔርን ማንነት የሚገልጽ አባባል ነው (ወካይ ዘይቤ)። ስሜ እንዲታሰብበት እንዲከብርበት በወሰንኩት ስፍራ ወይም ስሜን እንዲታከብሩ በመረጥኩት ሥፍራ

• ወደ መሠዊያዬ በደረጃ አትውጣ

ወደ ላይ ለመውጣት ደረጃ ያለውን መሰዊያ ለእኔ አትሥራ

• ኃፍረተ ሥጋህ በእርሱ እንዳይገለጥ

ራቁትህን እንዳትሆን


Chapter 21

1 የምትመሠርታቸው ድንጋጌዎች እነዚህ ናቸው፦ 2 አገልጋይ ብትገዛ፣ ስድስት ዓመት ያገልግልህና በሰባተኛው ዓመት ያለ ክፍያ ነጻ ይውጣ። 3 ከመጣ፣ ብቻውን ነጻ ይውጣ፤ ሚስት ያገባ ከሆነ፣ ሚስቱም ዐብራው ነጻ ትውጣ። 4 ጌታው ሚስት አጋብቶት ከሆነና እርሷም ወንዶች ወይም ሴቶች ልጆችን ከወለደችለት፣ ሚስቲቱና ልጆቿ የጌታዋ ይሆናሉ፤ ባልዮው ግን ብቻውን በነጻ ይሂድ። 5 ግን አገልጋይ፣ “ጌታዬን፣ ሚስቴንና ልጆቼን እወድዳለሁ፤ ነጻ ወጥቼ አልሄድም” ቢል፣ 6 ውደ ዳኞች ይውስደው፥ ወደ በሩ ወይም ወደ መቃኑ ወስዶም ጆሮውን በወስፌ ይብሳው፤ ከዚያም አገልጋይ ጌታውን ለዘለዓለም ያገለግለዋል። 7 ሰው ሴቶ ልጁን በአገልጋይነት ቢሸጣት፣ እንደ ወንዶቹ አገልጋዮች በነጻ መሄድ የለባትም። 8 ለራሱ የመረጣትን ጌታዋን ደስ ባታሰኝ፣ በዎጆ ይልቀቃት። ለባዕዳን እንዲሸጣት መብት የለውም፤ ምክንያቱም አታልሎአታል። 9 ለልጁ አያያዝ ያድርግለት። 10 ሌላ ሚስት ቢያጋባውም፣ የመጀመሪያዋን ሚስቱን ምግብ፥ ልብስ፣ ወይም ቊሳዊ መብት ማጕደል የለበትም። 11 ነገር ግን እነዚህን ሦስት ነገሮች የማይሰጣት ቢሆን፣ ያለ ምንም የገንዘብ ክፍያ በነጻ መሄድ ትችላለች። 12 ሰው ሰውን ቢደበድብና ቢገድል፣ ሊሞት ይገባዋል። 13 ሰውየው ዐስቦ ሳይሆን ድንገት አድርጎት ከሆነ፣ የሚሸሽበት ስፍራ አዘጋጃለሁ። 14 አንድ ሰው ባልንጀራውን ሆነ ብሎ በተንኮል ቢያጠቃውና ቢገድለው፣ ከእግዚአብሔር መሠዊያም እንኳ ተወስዶ ይገደል። 15 ወይም እናቱን የሚመጣ ይገደል። 16 የሚጠልፍና የሚሸጥ፣ ወይም የተጠለፈው ሰው በእጁየሚገኝበት ይገደል። 17 ወይም እናቱን የሚሳደብ ይገደል። 18 ቢጣሉና እንደኛው ሌላውን በድንጋይ ወይም በቡጢ ቢመታው፣ የተመታው ሰውም ባይሞትና ዐልጋው ላይ ቢቀር፤ 19 በኋላም ቢያገግምና በትሩን ተደግፎ በአካባቢው መንቀሳቀስ ቢችል፣ ለባከነበት ጊዜ የመታው ሰውን ይክፈል፤ ያገገመበትንም በሙሉ ይክፈል። ነገር ግን ያ ሰው የነፍስ ተጠያቂ አይደለም። 20 አንድ ሰው ወንድ ወይም የሴት አገልጋዩን በበትር ሲመታና አገልጋዩም ከድብደባው የተነሣ ቢሞት፥ ያ ሰው መቀጣት አለበት። 21 ነገር ግን አገልጋዩ አንድ ወይም ሁለት ቀን በሕይወት ቢቆይ፣ ጌታው መቀጣት የለበትም፤ አገልጋዩ የግል ንብረቱ ነውና። 22 ሰዎች ቢጣሉና ነፍሰ ጡር ሴት ቢጎዱ፣ እርሷም ብትጨነግፍ፣ ሆኖም ሌላ ጉዳት ባይደርስባት፣ በደለኛው ሰውዬ የሴትዮዋ ባል የሚጠብቅበትንና ዳኞቹ የሚወስኑትን መክፈል አለበት። 23 ጉዳት ካደረሰ ግን፣ ሕይወትን ለሕይወት፣ 24 ዐይንን ለዐይን፣ ጥርስን ለጥርስ፣ እጅን ለእጅ፣ እግርን ለእግር፣ 25 ቃጠሎን ለቃተሎ፣ ቊስልን ለቊስል፣ ወይም ግርፋትን ለግርፋት በቅጣት ታስከፍላለህ። 26 አንድ ሰው የወንድ ወይም የሴት አገልጋዩን ዐይን ቢመታና ቢያጠፋው፣ አገልጋዩን ስለ ዐይኑ ካሣ ነጻ ሊያደርገው ይገባል። 27 የወንድ ወይም የሴት አገልጋዩን ጥርስ ቢያወልቅ፣ አገልጋዩን ለጥርሱ ካሣ ነጻ ሆኖ እንዲሄድ ማድረግ አለበት። 28 በሬ አንድን ሰው ወይም ሴት ቢወጋና የሞት አደጋ ቢያደርስ፣ በሬው በድንጋይ ይወገር፣ ሥጋውም አይበላ፤ የበሬው ባለቤት ግን ከተጠያቂነት ነጻ ይሁን። 29 ግን በሬው የመዋጋት ልማድ ከቀድሞ ጀምሮ ካለበትና ባለቤቱ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶት በሬውን ሳይጠብቀው ቀርቶ፣ በሬው አንድ ወንድ ወይም ሴት ወግቶ ቢገድል፣ ያ በሬ በድንጋይ ይወገር፤ ባለቤቱም በሞት ይቀጣ። 30 ለሕይወቱ ካሣ እንዲከፍል ካስፈለገ፣ የተጠየቀውን ይክፈል። 31 በሬው የአንድን ሰው ወንድ ወይም ሴት ልጅ ቢወጋ፣ የበሬው ባለቤት ይህ ሕግ የሚጠብቅበትን ያድርግ። 32 ወንድ ወይም ሴት አገልጋይን ቢወጋ፣ የበሬው ባለቤት ሠላሳ የብር ሰቅል ለአገልጋዩ ጌታ መክፈልና በሬውም በድንጋይ መወገር አለበት። 33 ሰው ጕድጓድ ቢከፍት ወይም ቢቆፍርና ሳይደፍነው ቀርቶ በሬ ወይም አህያ ቢገባበት፣ 34 ባለቤት ለጠፋው መክፈል ይኖርበታል። ለሞተው እንስሳ ባለቤት ገንዘብ መክፈል አለበት፤ የሞተው እንስሳም የእርሱ ይሆናል። 35 የአንድ ሰው በሬ የሌላ ሰውን በሬ ቢወጋና ቢሞት፣ የበሬዎቹ ባለቤቶች በሕይወት ያለውን በሬ ሽጠው የተሸጠበትንና የሞተውንም በሬ ይካፈሉ። 36 ነገር ግን በሬው ከቀድሞ ጀምሮ የመውጋት ልማድ ያለበት መሆኑ ከታወቀና ባለቤቱም ያልጠበቀው ከሆነ፣ በበሬው ፈንታ በሬውን መክፈል አለበት፤ የሞተው እንስሳም የእርሱ ይሆናል።



Exodus 21:1

አጠቃላይ ምልከታ፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል • በፊታቸው የምታደርገው ሥርዓት

ለእስራኤላውያን የምትሰጣቸው ህግ ወይም ለእስራኤላውያን የምትነግራቸው ደንብ

Exodus 21:2

አጠቃላይ ምልከታ፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤላውያን ማድረግ ያለባቸውን ነገር በሙሴ በኩል ይናገራል •ብቻውን መጥቶ እንደሆነ ብቻውን ይውጣ

ብቻውን የሚለው ሀረግ በአንዳንድ ቋንቋዎች ግልጽ ላይሆን ይችላል። ስለሆነም ገላጭ ሊያስፈልገው ይችላል። አማራጭ ትርጉም፦ ባሪያ እንዲሆንህ አንተ በገዛኸው ጊዜ ሚስት ያላገባ ከሆነ ወይም እርሱን ባርያ ስታደርገው ሚስት ያላገባ ከሆነ ወይም ሚስት ያገባው አንተ ባርያ አድርገህ ከገዛኸው በኋላ ከሆነ።

• ብቻውን

“ያለ ሚስት” ወይም “ሚስት ሳያገባ”

• ከሚስቱ ጋር መጥቶ እንደሆነ

ባርያ ከመሆኑ በፊት አግብቶ ከሆነ ወይም በባርነት ከመገዛቱ በፊት ባለትዳር ከሆነ

Exodus 21:5

• አርነት አልወጣም ብሎ ቢናገር ብሎ ቢናገር

ብሎ ነጻ መውጣት ባይፈልግ ወይም ብሎ አለመፈለጉን በግልጽ ብናገር

• ጆሮውን በወስፌ ይብሳው

“ወስፌ” በጊዜው በእስራኤላውያን ባህል የተለመደው ጆር መብሻ መሳሪያ ነበር። ዛሬም እንደየህብረተሰቡ የመብሻ መሳሪያ መተካት ይቻላል። ስለሆነም በአማራጭ ጆሮውን በመብሻ ይብሳው ማለት ይቻላል።

• ለዘላለምም ባሪያው ይሁን

እስከ ዕድሜ ልክ ወይም እስኪ ሞት ድረስ

Exodus 21:7

• በዎጆ ይስደዳት

ተመልሳ በሕዝብዋ ትዋጅ ወይም አባቷ መልሶ እርሷን እንዲገዛት መፍቀድ አለበት

• ይሸጣት ዘንድ አይገባውም

ለባዕድ ሊሸጣት አይችልም ወይም ለባዕድ የመሸጥ ሥልጣን የለውም

• ስለ ናቃት

የማይገባ ነገር ስላደረገባት ወይም ስላታለላት

Exodus 21:9

• ለልጁም ብድራት

ሚስት ትሆንለት ዘንድ ለልጁ ቢሰጣት ወይም ልጁ እንዲያገባት ቢፈልግ

• መኖዋን ልብስዋንም ለምንጣፍዋም ተገቢውን አያጕድልባት

ለመጀመሪያ ሚስቱ ምግብ፥ ልብስ እና ቀድሞ የነበራትንም የጋብቻ መብት አይከልክላት

• መኖዋን . . . አያጕድልባት

የሚገባትን የምግብ አቅርቦት አያቋርጥባት

• ለምንጣፍዋም ተገቢውን አያጕድልባት (አይነኬ ዘይቤ)

በባልና ሚስት መካከል ያለውን የተራክቦ ግንኙነት አያቋርጥ ወይም አይከልክላት

Exodus 21:12

• ሰው ሰውን ቢመታ

ሰው ሰውን ቢገድል ወይም ሰውን ደብድቦ የሚገድል

• እርሱ ፈጽሞ ይገደል

ይህንን ተደራጊ ግስ በአድራጊ ግስ መተርጎም ይቻላል፦ ይህን ሰው በርግጥ መግደል አለብህ ወይም ይህ ሰው መሞት አለበት

• ባይሸምቅበትም

ሆን ብሎ ደፈጣ በማድረግ ሳይሆን ወይም ጉዳት ለማድረስ በልቡ ባያስብ ወይም ባያቅድ

• የሚሸሽበት ስፍራ እኔ አደርግልሃለሁ

ሸሽቶ በማምለጥ በሰላም የሚኖርበትን ስፍራ እኔ አዘጋጅለታለሁ

• ባልጀራውን በተንኮል ቢገድለው

ሆን ብሎ ወይም አውቆ ሌላ ሰው ቢገድል

• እንዲሞት ከመሠዊያዬ አውጥተህ ውሰደው

ሕይወቱን ለማዳን ወደ መሠዊያዬ ሸሽቶ ቢሄድ በሞት ይቀጣ

Exodus 21:15

• አባቱን ወይም እናቱን የሚመታ ፈጽሞ ይገደል

ይህን ዐረፍተ ነገር በአድራጊ ግስ ሲንተረጉም፦ ማንም አባቱን ወይም እናቱን ቢመታ አንተ እርሱን መግደል አለብህ

• ፈጽሞ ይገደል

ፈጽሞ መሞት አለበት

• በእጁ ቢገኝ

“እጅ” በወካይ ዘይቤነት የቀረበ ስለሆነ የአንድን ሰው ሙሉ ማንነቱን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ በአንተ ቁጥጥር ሥር

• እርሱ ፈጽሞ ይገደል

በሞት ይቀጣ ወይም ፈጽሞ ይገደል

• አባቱን ወይም እናቱን የሚሰድብ ፈጽሞ ይገደል

አባቱን ወይም እናቱን የሚራገም ወይም በአባቱና በእናቱ ላይ ክፉ ቃል የሚናገር

Exodus 21:18

• ታምሞ በአልጋው ላይ ቢተኛ

የተመታው ሰው ታሞ በአልጋ ላይ ቢውል ወይም አልጋ ላይ ተኝቶ ቢቀር

• ተነሥቶም በምርኩዝ

በኋላም ተነስቶ ወይም ህመሙ ሲሻለው ወይም በትር እየተመረኰዘ መራመድ ቢችል

• ምርኩዝ

ከእንጨት ወይም ከብረት የተሰራ የጉዞ መደገፊያ

• ተግባሩን ስላስፈታው

ሰውዬው በመታመሙ ምክንያት የባከነውን የሥራ ጊዜ ወይም ሥራ ያልሰራበትን ቀናት የሚመለከት ነው።አማራጭ ትርጉም፦ ሥራ ሳይሰራ ከንቱ ያሳለፈው ጊዜ

• ገንዘብ ይከፍለው ዘንድ

“የመታው ሰው ካሣ ይክፈለው” ወይም “የመታው ሰው የህክምና ወጪ ሊከፍለው ይገባል”

Exodus 21:20

• ቢሞትበትም

አንድ ሰው በምቱ ምክንያት ቢሞትበት” ወይም “ጌታው ባርያውን ቢመታና ቢሞትበት”

• ፈጽሞ ይቀጣ

ያ ሰው መቀጣት ይገባዋል ወይም ያንን ሰው መቅጣት አለብህ

• ገንዘቡ ነውና አይቀጣ

በትርጉሙ ውስጥ ባርያው ለባለቤቱ ንብረቱ ወይም ሀብቱ እንደሆነ መገለጽ አለበት። አማራጭ ትርጉም፦ ምክንያቱም ጌታው ውድ የሆነውን ባርያውን በማጣቱ ተጎቷል

Exodus 21:22

• ልጁን እስክትጨነግፍ ቢገፉአት ባትጎዳ

ህጻኑን ቢያስወርዳት ወይም ያለጊዜው ተወልዶ ቢሞትና በሴትዮዋ ላይ ሌላ ምንም ጒዳት ሳይደርስ ቢቀር

• የሴቲቱ ባል የጫነበትን ያህል ካሳ ይስጥ

በሌላ አገላለጽ፦ አጥፊው ሰው መቀጣት አለበት ወይም ያጠፋው ሰው ተገቢውን ካሳ መክፈል አለበት

• ፈራጆቹም እንደ ፈረዱበት ይክፈል

ዳኞች የፈረዱበትን ወይም የወሰኑበትን ካሳ መክፈል አለበት

• ጕዳት ግን ቢያገኛት ሕይወት በሕይወት ዓይን በዓይን . . .

ሴትዮዋ ብትጎዳ የጎዳትም ሰው በተመሳሳይ መልኩ መጎዳት አለበት። አማራጭ ትርጉም፦ ሰውዬው ለሕይወቷ ሕይወቱን፥ ለዓይኗ ዓይኑን መክፈል ወይም መጎዳት አለበት

Exodus 21:26

• ሰውም

የባርያ ጌታው ወይም አሳዳሪው

• አርነት ያውጣው

ለበደለው በደል ካሣ እንዲሆን ባሪያውን ነጻ ይልቀቅ

Exodus 21:28

• በሬ ወንድን ወይም ሴትን . . . ቢወጋ

የአንድ ሰው በሬ አንድን ሰው በቀንዱ ወግቶ ቢገድል

• በሬው ይወገር

በሬው በድንጋይ ተወግሮ ይሙት ወይም በሬውን በድንጋይ ወግራችሁ ግደሉት

• ሥጋውም አይበላ

በሌላ አገላለጽ፦ የበሬውን ሥጋ አትብሉ ወይም የበሬው ሥጋ አይበላ

• የበሬው ባለቤት ግን ንጹሕ ነው

በሌላ አገላለጽ፦ የበሬው ባለቤት በነጻ ይለቀቅ ወይም የበሬውን ባለቤት በነጻ ልቀቁት አይጠየቅ

• ባለቤቱ ደግሞ ይገደል

የበሬው ባለቤት ወይም ባለ ንብረቱ በሞት ይቀጣ ወይም የበሬውን ባለቤት ወይም ባለ ንብረቱን ግደሉት

• ከእርሱ ግን ካሳ ቢፈልጉ

ተጎጂዎች ካሳ ክፊያ ቢፈልጉ የበሬው ባለቤት ሕይወቱን ለማዳን ቢፈልግ ዳኞች የወሰኑበትን መክፈል አለበት። በትርጉሙ ውስጥ ይህ ግልጽ ሆኖ መታየት አለበት። አማራጭ ትርጉም፦ የበሬው ባለቤት ሕይወቱን ለመዋጀት ወይም ከሞት ለመትረፍ ካሣ እንዲከፍል ከተፈቀደለት ወይም ከተስማሙ ካሣውን በሙሉ መክፈል አለበት።

Exodus 21:31

• ወንድን ልጅ ቢወጋ ሴትንም ልጅ ቢወጋ

ያ በሬ ወይም የዚያ ሰው በሬ ወንድ ወይም ሴት ልጅ ወግቶ ቢገድል

• ሠላሳ የብር ሰቅል

330 ግራም ብር ይስጥ፤ አንድ ሰቅል 11 ግራም ብር ይመዝናል።

• በሬውም ይወገር

በሬውን በድንጋይ ወግራችሁ ግደሉት ወይም በሬው በድንጋይ ተግሮ ይሙት

Exodus 21:33

• ሰውም ጕድጓድ ቢከፍት

አንድ ሰው የጒድጓድ መክደኛ ቢያነሣ ወይም ጒድጓድ ቆፍሮ ሳይከድነው ቢተው

• ዋጋቸውን ለባለቤታቸው ይክፈል

የበሬው ባለቤት ይጉዳቱን ካሳ ማግኘት አለበት። አማራጭ ትርጉም፦ ለበሬው ባለቤት ለሞተው እንስሳ ምትክ ካሳ ይከፈለው

• የሞተውም ለእርሱ ይሁን

ለሞተው እንስሳ ምትኩን የከፈለው ሰው የሞተውን እንሳሳ ለራሱ ወስዶ የፈለገውን ማድረግ ይችላል። የዚህ ክፍል የመልዕክቱ ዋና ሀሳብ ግልጽ ሆኖ መውጣት አለበት። አማራጭ ትርጉም፦ የሞተው እንስሳ ለጉድጓዱ ባለቤት ይሆናል ወይም የሞተውን እንስሳ ለራሱ ማስቀረት አለበት

Exodus 21:35

• ዋጋውንም በትክክል ይካፈሉ

የበሬውን ዋጋ በጋራ ይክፋፈሉ ወይም ገዘቡን አብረው ይካፈሉ”

• ተዋጊ መሆኑ ቢታወቅ

በሌላ አገላለጽ፦ በሬው ተዋጊ መሆኑን ሰዎች የሚያውቁ ከሆነ ወይም የበሬው ባለቤት በሬው ተዋጊ መሆኑን የሚያውቅ ከሆነ

• ባለቤቱም ባይጠብቀው

የበሬው ባለቤት በሬው በአግባቡ ባይጠብቀው ወይም ከአጥር ውስጥ እንዳይወጣ ባያደርግ

• በሬውን በበሬው ፈንታ ይስጥ

የገደለው በሬ ባለቤት በሬው ለሞተበት ሰው በሬ መካስ አለበት። ስለሆነም በትርጉም ውስጥ ይህ ሀሳብ በግልጽ መታየት አለበት። አማራጭ ትርጉም፦ በሬው ለሞተበት ሰው አንድ በሕይወት ያለ በሬ ካሣ መክፈል አለበት


Chapter 22

1 ሰው በሬ ወይም በግ ቢሰርቅና ቢያርደው ወይም ቢሸጠው፣ ለአንድ በሬ ዐምስት በሬ፣ ለአንድ በግም ዐምስት በግ መክፈል አለበት፥ 2 ሌባ በር ሰብሮ ሲገባ ቢገኝና ተደብድቦ ቢሞት፣ በማንም ሰው ላይ የደም ዕዳ አይኖርም። 3 ነገር ግን ሰብሮ ከመግባቱ በፊት ፀሐይ ከወጣ፣ በገደለው ሰው ላይ የደም ተጠያቂነት ይኖራል። ሌባ የሰረቀውን መመለስ አለበት። ምንም ነገር ከሌለው፣ የሰረቀውን እንዲከፍል እርሱ ራሱ መሸጥ ይኖርበታል። 4 ሆነ አህያ ወይም በግ ቢሆን የተሰረቀው እንስሳ በሕይወት እርሱ ዘንድ ከተገኘ፣ ዕጥፉን መልሶ መክፈል አለበት። 5 ሰው ከብቱን መስክ ላይ ወይም የወይን ዕርሻ ውስጥ አሰማርቶ ቢለቅቀውና በሌላ ሰው ዕርሻ ውስጥ ገብቶ ቢግጥ፣ ምርጥ ከሆነው ከራሱ መስክና የወይን ዕርሻ መካስ ይኖርበታል። 6 እሳት ቢነሣና በእሾኾችም ውስጥ ቢዛመት፣ ክምሩም፣ ያልታጨደውም እህል ወይም ዕርሻው ቢቃጠል፣ እሳቱን ያቀጣጠለው ሰው ካሣ ይካሥ። 7 ሰው እንዲጠበቅለት ገንዘቡን ወይም ዕቃውን ለጎረቤቱ ቢሰጥ፣ በዐደራ ያስቀመጠውንም ከሰውዬው ቤት ሌባ ቢሰርቀውና ሌባውም ቢገኝ፣ ያ ሌባ ዕጥፍ መክፈል አለበት፤ 8 ባይገኝ ግን፣ የቤቱ ባለቤት እጁን በጎረቤቱ ንብረት ላይ መዘርጋቱንና አለመዘርጋቱን ለማየት፣ በዳኞች ፊት ሊቀርብ ይገባል። 9 ስለ በሬ፣ ስለ አህያ፣ ስለ በግ፣ ስለ ልብስ ወይም አንድ ሰው፣ “ይህ የእኔ ነው” ስለሚለው ስለ ማንኛውም የጠፋ ነገር የሚነሣ ክርክር ሁሉ፣ የሁለቱም ወገን አቤቱታ በዳኞች ፊት መቅረብ አለበት። ዳኞች በደለኛ ሆኖ ያገኙት ሰው ለጎረቤቱ ዕጥፍ መክፈል ይኖርበታል። 10 አንድ ሰው አህያ፣ በሬ፣ በግ፣ ወይም ማንኛውም እንስሳ እንዲጠበቅለት ለጎረቤቱ በዐደራ ቢሰጥና እንስሳው ቢሞት፣ ወይም ጕዳይ ቢደርስበት፣ ወይም ማንም ሳያይ ቢወሰድ፣ 11 ሰው በጎረቤቱ ንብረት ላይ እጁን መዘርጋቱን ወይም አለመዘርጋቱን ለመለየት፣ ሁለቱም በእግዚአብሔር ፊት መማል አለባቸው። ባለቤቱ ይህን ሊቀበል ይገባል፤ ሌላውም ሰው ካሣ አይክሥም። 12 ነገር ግን እንስሳው ከእርፍሱ ተሰርቆ ከሆነ፣ ሌላው ሰው ለባለቤቱ ካሣ መካሥ አለበት። 13 አንድን እንስሳ አውሬ ቢዘነጥለው፣ ሌላው ሰውዬ እንስሳውን ማስረጃ አድርጎ ያቅርብ። ለተዘነጣጠለው እንስሳ ካሣ መክፈል የለበትም። 14 አንድ ሰው ከጎረቤቱ እንስሳ ቢዋስና እንስሳው ባለቤቱ በሌለበት ቢጎዳ ወይም ቢሞት፣ ሌላው ሰውዬ ካሣ መካሥ አለበት። 15 ባለቤቱ ካለበት ከሆነ ግን፣ ሌላው ሰውዬ ካሣ መክፈል የለበትም፤ እንስሳ ተከራይቶ የነበረ ከሆነ፣ በተከራየበት ዋጋ ይከፈላል። 16 አንድ ሰው ያልታጨች ልጃገረድን ቢያታልልና ዐብሯት ቢተኛ፣ ለዚህ ተገቢ የሆነውን ማጫ ከፍሎ ሚስቱ ሊያደርጋት ይገባል። 17 አባቷ በሚስትነት አልሰጥህም ካለው፣ ልጃገረዶች ማጫ ከሚከፈለው ጋር እኩል የሆነ ገንዘብ መክፈል አለበት። 18 መተተኛ ሴት በሕይወት እንድትኖር አትፍቀድ። 19 ከእንስሳት ጋር የወሲብ ግንኙነት የሚያደርግ መምት አለበት። 20 ከእግዚአብሔር በቀር ለማንኛውም ባዕድ አምላክ መሥዋዕት የሚሠዋ ፈጽሞ መጥፋት ይኖርበታል። 21 መጻተኛውን አትበድሉት ወይም አታስጨንቁት፤ እናንተም በግብፅ ምድር መጻተኞች ነበራችሁና። 22 ማንኛዋንም መበለት ወይም አባትና እናት የሌለውን ልጁ ማስጨነቅ የለባችሁም። 23 የምታስጨንቋቸው ከሆነና እነርሱም ወደ እኔ ከጮኹ፤ እኔ እግዚአብሔር ጩኸታቸውን እሰማለሁ። 24 ቊጣዬ ይቀጣጠላል፤ በሰይፍም እገድላችኋለሁ፤ ሚስቶቻችሁ መበለታት፣ ልጆቻችሁም አባት ዐልባዎች ይሆናሉ። 25 ከሕዝቤ መካከል ድኻ ከሆኑት ለአንዱ ገንዘብ ብታበድሩ፣ እንደ አራጣ አበዳሪ አትሁኑበት ወይም ወለድ አታስከፍሉት። 26 የጎረቤትህን ልብስ በመያዣነት ብትወስድ፣ ፀሐይ ከመግባቷ በፊት ልትመልስለት ይገባል። 27 ሰውነቱን የሚሸፍንበት ልብሱ እርሱ ብቻ ነውና። ምን ሌላ ልብስ ለብሶ መተኛት ይችላል? ወደ እኔ ሲጮኽ፣ ርኅሩኅ ነኝና እሰማዋለሁ። 28 ፈራጆችንም አትስደብ፤ የሕዝብህን አለቃም አትርገም። 29 ወይም ከወይን ጭማቂዎችህ የምታቀርባቸውን ስጦታዎች ማዘግየት የለብህም። የወንድ ልጆችህንም በኵር ለእኔ መስጠት አለብህ። 30 በበጎችህ ላይም ይህንኑ ማድረግ ይኖርብሃል። ልጆቹ ሰባት ቀን ክአእናቶቻቸው ጋር መቆየት ይችላሉ፤ በስምንተኛው ቀን ግን ለእኔ መስጠት አለብህ። 31 ለእኔ ቅዱስ ሕዝብ ትሆናላችሁ። ስለዚህ መስክ ላይ አውሬ የዘነጣጠለውን ሥጋ ለውሾች ጣሉት፣ ልትበሉት አይገባም።



Exodus 22:1

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• ቢሰርቅ

በሌላ አገላለጽ፦ አንድ ሰው ሌባ ሆኖ ቢገኝ ወይም አንድ ሰው ሰርቆ ቢገኝ

• ሌባው ቤት ሲምስ ቢገኝ

በሌላ አገላለጽ፦ አንድ ሌባ የአንድ ሰው ቤት ሰብሮ ቢገባ

• እርሱም እስኪሞት ቢመታ

በሌላ አገላለጽ፦ አንድ ሰው ቢመታውና ሌባው ቢሞት

• በመታው ሰው ላይ የደም ዕዳ አይሆንበትም

በሌላ አገላለጽ፦ ተከላካዩ ወይም ሌባውን መቶ የገደለው ሰው ለፈሰሰው ደም ወይም በመግደሉ ተጠያቂ አይሆንም

• ፀሐይ ግን ከወጣችበት የደም ዕዳ አለበት

በሌላ አባባል፦ ፀሐይ ከወጣ በኋላ ወይም ብርሃን እያለ ሌባው ተመትቶ ቢገደል ግን ተከላካዩ በግድያው ተጠያቂ ይሆናል

• ሌባው የሰረቀውን ይመልስ

ሌባው የሰረቀውን መክፈል አለበት ወይም ሌባው በሰረቀው ንብረት ምትክ ክፊያ መስጠት አለበት

• የሚከፍለውም ቢያጣ ስለ ሰረቀው ይሸጥ

ምንም ከሌለው ግን የሰረቀውን ይከፍል ዘንድ ራሱ በባርነት ይሸጥ

• የሰረቀው ደኅና ሆኖ በእጁ ቢገኝ

ሌባው የሰረቀው እንስሳ ሕያው ሆኖ ቢገኝ ወይም በሕይወት ቢገኝ

• የሰረቀውን ያህል ሁለት እጥፍ ይክፈል

ለያንዳንዱ እንስሳ ዕጥፍ ዋጋ ወይም ሁለት እንስሳ ይክፈል

Exodus 22:5

• ማንም ሰው ወደ እርሻ ወይም ወደ ወይን ስፍራ ከብቱን ቢነዳው

አንድ ሰው እንስሶቹ በእርሻው ወይም በመስክ ወይም በወይን ተክል ቦታ አሰማርቶ እያለ

• የሌላውንም እርሻ ቢያስበላ

እንስሶቹ ወደ ሌላ ሰው እርሻ ገብተው ሰብሉን ቢበሉት

• ከተመረጠ እርሻው ከማለፊያውም ወይኑ ይካስ

ከራሱ እርሻ ሰብል ወይም የወይን ቦታ ምርጡን መክፈል አለበት

Exodus 22:6

• እሳት ቢነሣ፥ እሾኽንም ቢይዝ

አንድ ሰው በእርሻው ውስጥ እሳት ቢያቀጣጥልና እሳቱ ወደ ቊጥቋጦ ተዛምቶ ቢሰራጭ

• ክምሩንም ወይም ያልታጨደውን እህል ወይም እርሻውን ቢያቃጥል

ወደ ሌላው ሰው እርሻ በመዛመት ያልታጨደውን ወይም ታጭዶ የተቀመጠውን ወይም የተከመረውን እህል ቢያቃጥል

• እሳቱን ያነደደው ይካስ

እሳቱን ያቀጣጠለው ሰው ካሣ ይክፈል

Exodus 22:7

• አደራ ቢያኖር

እንዳይጠፋበት ወይም እንዳይሰረቅበት በአደራ ቢያስቀምጥ

• ከቤቱም ቢሰረቅ

በሌላ አገላለጽ፦ አንድ ሰው ወይም ሌባ ቢሰርቀው

• ሌባው ቢገኝ

በሌላ አገላለጽ፦ የሰረቀውን ሰው ብታገኘው ወይም ብታገኘው

• ሌባውም ባይገኝ ባለቤቱ ወደ ፈራጆች ይቅረብ

ሌባው ካልተገኘ ግን ዕቃውን በዐደራ የተቀበለው ሰው ዳኞች ፊት ይቅረብ /ይምጣ/

• እጁንም በባልንጀራው ከብት ላይ እንዳልዘረጋ ይማል

“እጁን . . . እንዳልዘረጋ” የሚለው ዘይቤያዊ አነጋገር ነው። ይህን ዘይቤያዊ እነጋገር በተመሳሳይ ዘይቤያዊ ንግግር መትርጎም የሚቻል ከሆነ መተረጎም ጥሩ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የዚያን ሰው ንብረት ራሱ አለመስረቁን በመሐላ ያረጋግጥ

• ክርክራቸው ወደ ፈራጆች ይድረስ

በሁለቱ መካከል ክርክር ቢነሣ ባለ ጉዳዮቹ ነገሩን ለዳኞች ያቅርቡት

Exodus 22:10

• የእግዚአብሔር መሐላ በሁለታቸው መካከል ይሁን

እንስሳውን ሰርቀሃል ተብሎ የተከሰሰው ሰው አለመስረቁን በመሀላ ያረጋግጥ። የእንሳሳው ባለቤት ደግሞ የሰውየውን መሀላ መቀበል አለበት። በሌላ አገላልጽ፦ እንስሳውን በአደራ የተቀበለው ሰው በእግዚአብሔር ፊት ይማል እንዲሁም የእንስሳው ባለቤት መሀላውን ይቀበል

• ከእርሱም ዘንድ ቢሰረቅ

በሌላ አገላለጽ፦ እንስሳው ከባለአደራው የተሰረቀ ከሆነ

• ተቧጭሮም ቢገኝ

በሌላ አገላለጽ፦ እንስሳው በአውሬ ተሰብሮን ተበልቶ ከሆነ

• በመቧጨሩም ምክንያት አይክፈል

አውሬ ስለ ገደለውም ወይም ስለበላው ካሳ አይክፈል።

Exodus 22:14

• ፈጽሞ ይክፈለው

በውሰት ለሰጠው ሰው ካሳ መክፈል አለበት ወይም በውሰት ለሰጠው ሰው ሌላ እንስሳ በምትክ መስጠት አለበት

• ባለቤቱ ግን ከእርሱ ጋር ቢኖር አይክፈል

ባለቤቱ ከእንስሳው ጋር ከሆነ ግን ተበዳሪው መክፈል የለበትም

• ቢከራየው በክራዩ ይግባ

እንስሳውን የተከራየው ሰው ከክራይ ገንዘብ ይልቅ ምንም ዓይነት ካሳ መክፈል የለበትም። የክራዩ ገንዘብ ክሳርውን ይሸፍንለትታል ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ለኪራይ የተከፈለው ገንዘብ ጒዳቱን ወይም ኪሳራውን ያካክስለታል።

Exodus 22:16

• ሰው ያልታጨችውን ድንግል ቢያስታት

አንድ ሰው ያልታጨችን ልጃገረድ ከእርሱ ጋር እንድትተኛ ቢያታልላት

• ያልታጨች

ለጋብቻ ያልታጨች ወይም ቃል ኪዳን ይላደረገች

• ከእርስዋም ጋር ቢተኛ (አይነኬ ዘይቤ)

ከእርሷ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት ቢፈጽም

• ማጫዋን ሰጥቶ

የሞራል ካሳ ከፍሎ ወይም የማጫ ዋጋ ከፍሎ

• ሚስት ያድርጋት

የሞራል ካሳ ከፍሎ ወይም የማጫ ዋጋ ከፍሎ

• ሚስት ያድርጋት

“ሚስት ያድርጋት” የተባለው አታሏት የደፈራት ወይም ክብረ ንጽህናዋን የወሰዳት”

Exodus 22:18

• ከእንስሳ ጋር የሚረክስ ፈጽሞ ይገደል

እዚህ ጋር “የሚረክስ” የሚለው በአይነኬ ዘይቤ የተገለጸ ሲሆን አንድ ሰው ከእንስሳ የሚፈጽመውን የግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚመለከት ነው። በሌላ አገላለጽ፦ “ከእንስሳ ጋር ግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚፈጽምን ሰው ፈጽማችሁ ግደሉ”

Exodus 22:20

• ከእግዚአብሔር በቀር ለአንዳች አምላክ የሚሠዋ ፈጽሞ ይጥፋ

ከእግዚአብሔር ሌላ ለማንኛውም አምላክ መሥዋዕት የሚያቀርብ በሞት ይቀጣ ወይም ግደሉት

• ስደተኛውን አትበድለው

መጻተኛውን ወይም እንግዳ ሰው አትበድል ወይም አታስጨንቅ

Exodus 22:22

• መበለቲቱንና ድሀ አደጎቹን አታስጨንቁአቸው

በሌላ አገላለጽ፦ ባል የሞተባትን ሴት እና አባትና እናት የሞቱበትን ድኻ ዐደግ አታጒላሉ” ወይም “ባል የሞተባትን ሴት እና ወላጅ አጥ ድኻ ዐደጉን እኩል አስተናግድ”

• መበለት

ባሏ የሞተባት ሴት

• ድሀ አደጎቹን

አባትና እናት የሞተበት

• በሰይፍም አስገድላችኋለሁ

በጦርነት ወይም በተለየ አደጋ እንድትሞቱ አደርጋችኋለሁ

Exodus 22:25

• ገንዘብ ብታበድረው

ለአንድ ሰው ገንዘብ ብታበድር

• እንደ ባለ አራጣ አትሁን

እንደ ገንዘብ አበዳሪ ወለድ ጨምሮ እንዲከፍልህ አትጠይቀው

• የባልንጀራህን ልብስ ለመያዣ ብትወስድ

የባልንጀራህን ወይም የጓደኛህን ልብስ መያዣ አድርገህ ብትይዝ

• ሥጋውን የሚከድንበት እርሱ ብቻ ነውና

ምክንያቱም ለሰውነቱ መሸፈኛ ወይም ለብርድ መከላከያነት ያለው ልብስ ያ ብቻ ነው

• የሚተኛበትም ሌላ የለውምና

ምክንያቱም ሌላ ለብሶ የሚተኛበት ወይም የሚያድረበት የለውም

Exodus 22:28

• ፈራጆችን አትስደብ

በእግዚአብሔር (ያህዌ) ላይ የስድብ ቃል አትናገር ወይም አታሰማ

• የሕዝብንም አለቃ አትርገመው

የሕዝብንም አለቃ አትርገመው” ወይም “የህዝብህን መሪ እንድረግመው እግዚአብሔርን አትጠይቅ

Exodus 22:29

• ነዶህንም የወይንህንም ጭማቂ ለማቅረብ አትዘግይ

በሌላ አገላለጽ፦ “የእህልህን ወይም የወይን ጠጅህን መስዋዕት ለእኔ ከማቅረብ ወደ ኋላ አትበል”


Chapter 23

1 ማንም ሰው የሐሰት ወሬ እትናገር። ሐሰተኛ ምስክር ለመሆን ከክፉ ሰው ጋር አትተባበር። 2 ክፋት ለመፈጸም ሕዝብን አትከተል፤ ወይም ፍትሕን ለማጣመም ከሰዎች ጋር ተባብረህ ምስክርነት አትስጥ። 3 ድኻውን በሙግቱ አታድላለት። 4 በሬ ወይም አህያ ጠፍቶ ብታገኘው መልስለት። 5 የሚጠላህን ሰው አህያ እንደ ተጫነ ከጭነቱ ሥር ወድቆ ብታየው፣ ያን ሰው ትተኸው አትሂድ። አህያውን ለማንሣት ልታግዘው ይገባል። 6 ጊዜ ለድኻው ወገንህ የሚሰጠውን ፍትሕ አታጣምም። 7 በሐሰት ክስ ከሌሎች ጋር አትተ ባበር፤ ንጹሑንም ወይም ጻድቁንም አትግደል፤ እኔ ኀጢአተኛውን ንጹሕ አላደርግምና። 8 አትቀበል፤ ጕቦ የሚያዩ ሰዎችን ያሳውራል፤ የታማኝ ሰዎችን ቃልም ያጣምማልና። 9 የመጻተኛነትን ስለምታውቁት፣ መጻተኛን አታስጨንቁ፤ እናንተም በግብፅ ምድር መጻተኞች ነበራችሁና። 10 ስድስት ዓመት በመሬትህ ላይ ዘር ዝራ፤ መከሩንም ሰብስብ። 11 በሰባተኛው ዓመት ግን በሕዝብህ መካከል ያሉ ድኾች መብላት እንዲችሉ ሳታርሰው ዕዳሪውን ተወው። ከድኾች የሚተርፈውንም የዱር እንስሳት ይበሉታል። በወይን ቦታዎችህና በወይራ ዛፎችህም ይህንኑ ታደርጋለህ። 12 ቀን ሥራህን ትሠራለህ፤ በሰባተኛው ቀን ግን ታርፋለህ። ይህን የምታደርገውም፦ በሬህ፣ አህያህ፣ የሴት አገልጋይህ ወንድ ልጅና መጻተኛው ሁሉ ዕረፍት እንዲያገኙና እንዲዝናኑ ነው። 13 የነገርኋችሁን ሁሉ ጠብቁ። የሌሎች አማልክትን ስም አትጥሩ፤ ወይም ስማቸው ከአፋችሁ አይሰማ። 14 በየዓመቱ ሦስት ጊዜ ልአእኔ በዓል ታከብራላችሁ። 15 በዓልን አክብር። ባዘዝሁህ መሠረት ሰባት ቀን ቂጣ ትበላለህ። በዚያ ጊዜ፣ ለዚህ በተወሰነው በአቢብ ወር በፊቴ ትቀርባለህ። ከግብፅ የወጣኸው በዚህ ወር ነበር። ነገር ግን በፊቴ ባዶ እጅህን መቅረብ የለብህም። 16 ላይ የዘራኸውን የእህልህን በኵራት፣ የመከርን በዓል አክብር። በዓመቱ መጨረሻ ምርትህን ከማሳ ስትሰበስብ፣ የመክተቻውን በዓል አክብር። 17 ዘንድ ያለ ወንድ ሁሉ በዓመት ሦስት ጊዜ በእኔ በእግዚአብሔር ፊት ይቅረብ። 18 የመሥዋዕቱን ደም እርሾ ካለበት ዳቦ ጋር ለእኔ አታቅርብ። በበዓሎቼ የሚቀርበው የመሥዋዕቴ ሥብ እስከ ንጋት ድረስ መቆየት የለበትም። 19 የመሬትህን ምርጥ ፍሬ በኵራት ወደ እኔ፣ ወደ አምላክህ ወደ እግዚአብሔር ቤት አምጣ። የፍየልን ግልገል በእናቱ ወተት አትቀቅል። 20 በመንገድ የሚጠብቅህንና ወዳዘጋጀሁልህ ስፍራ መርቶ የሚያስገባህን መልአክ በፊትህ እልካለሁ። 21 ተከተለው፤ ታዘዝለትም። ኀጢአትህን ይቅር አይልህምና አታስቆጣው። ስሜ በእርሱ ላይ ነው። 22 ድምፁን በእውነት ብትሰማና የምነግርህን ሁሉ ብታደርግ፣ ለጠላቶችህ ጠላት እሆናለሁ፤ የሚቃወሙህንም እቃወማለሁ። 23 መልአክ በፊትህ ይሄዳል፤ አንተንም ወደ አሞራውያንና ወደ ኢያቡሳውያን ምድር ያስገባሃል። እኔ እነርሱን አጠፋቸዋለሁ። 24 ለአማልክታቸው አትስገድ፤ አታምልካቸውም፤ ወይም ሕዝቡ እንደሚያደርጉት አታድርግ፤ ይልቁን ፈጽመህ ልታፈራርሳቸው፣ የድንጋይ ዐምዶቻቸውንም ልትሰባብራቸው ይገባል። 25 እኔን አምላክህን እግዚአብሔርን አምልክ። ይህን ካደረግህ፣ የምትባውንና የምትጠጣውን እባርካለሁ። በሽታንም ከመካከልህ አጠፋለሁ። 26 የምትጨነግፍ ወይም የምትመክን ሴት አትምርም። ለአንተ ረጅም ዕድሜ እሰጥሃለሁ። 27 ምድር ሕዝብ ላይ ማስፈራቴን እልካለሁ። የሚያጋጥሙህን ሰዎች ሁሉ እገድላለሁ። ጠላቶችህን ሁሉ ከፍርሀት የተነሣ ጀርባቸውን ወደ አንተ እንዲያዞሩ አደርጋለሁ። 28 ከነዓናውያንና ኬጤያውያንን ከፊትህ እንዲያበሯቸው ተርቦችን በፊትህ እሰድዳለሁ። 29 ወና እንዳትሆንና የዱር አራዊትም እጅግ እንዳበዙብህ፣ የምድሪቱን ኗሪዎች በአንድ ዓመት ውስጥ ከፊትህ አላባርራቸውም። 30 ነገር ግን አንተ እስክትበዛና ምድሪቱን እስክትወርሳት ድረስ በትንሽ በትንሹ አስወጣቸዋለሁ። 31 ከቀይ ባሕር እስከ ፍልስጥኤም ባሕር፣ ከምድር በዳውም እስከ ኤፍራጥስ ወንዝ ድረስ አደርገዋለሁ። በምድሪቱ ኗሪዎች ላይ ድል እንድትጎናጸፍ አደርጋለሁ፤ ከፊትህም ታባርራቸዋለህ። 32 ወይም ከአማልክታቸው ጋር ኪዳን አታድርግ። 33 እነርሱ በምድርህ ውስጥ መኖር አይገባቸውም፤ አልዚያ በእኔ ላይ ኀጢአት እንድትሠራ ያደርጉሃል። አማልክታቸውን ብታመልክ፣ ይህ በእውነት ወጥመድ ይሆንብሃል።”



Exodus 23:1

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• ሐሰተኛ ምስክርም ትሆን ዘንድ

ተንኰል ያለበትን ምስክርነት በመስጠት ወይም በሀሰት በመመስከር

• ብዙ ሰዎችን አትከተል

ይህ ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን አንድ ሰው ከብዙ ሰው ጋር በመስማማት ፍለጋቸውን መከተልን የሚያመለክት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ክፉ ለማድረግ የተሰባሰቡ ሰዎችን አትከተል ወይም ብዙ ሰዎች የሚፈልጉትን ለማድረግ ከእነርሱ ጋር አትተባበር

• ፍርድንም ለማጥመም

ፍትህን ወይም እውነተኛ ፍርድን ለማዛባት ወይም የህሊና ዳኝነት ለመካድ ወይም ላለመስማት

Exodus 23:4

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

Exodus 23:6

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• በሚምዋገትበት ጊዜ የድሀህን ፍርድ አታጥምም

በፍርድ አደባባይ ወይም በዳኝነት አድልዎ በማድረግ የድኻውን ፍርድ አታጣምበትብ ወይም አታዛባ

Exodus 23:10

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• ፍሬዋንም አግባ

ከእርሻ የምታገኘውን ምርት ሰብስብ

• ተዋት አሳርፋትም

ሳትርሳት እንዲሁ ተዋት፤ ምድርቱን አሳርፋት

• የሕዝብህም ድሆች ይበሉታል

ድሆች በእርሻው ውስጥ ራሱ የበሰለውን ምርት ይበሉ ዘንድ ምድርቱን ሳታርስ ተው። አማራጭ ትርጉም፦ በሕዝብህ መካከል የሚገኙ ድኾች ምግብ ያገኙ ዘንድ ወይም በወገንህ መካከል ያሉት ድኾች ከእርሷ ምግብ ያገኛሉ

Exodus 23:12

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• ያልኋችሁንም ነገር ሁሉ ጠብቁ

የነገርኳችሁን ሁሉ በጥንቃቄ አድምጡ

• በሬህና አህያህ ያርፉ ዘንድ

የሥራ እንስሳት እንዲያርፉ

• ለባሪያህም ልጅ ለመጻተኛውም ዕረፍት ይሆን ዘንድ

በሌላ አገላለጽ፦ በቤትህ የተወለደው ባሪያና መጻተኛው ወይም የሌላ አገር ሰው ያርፉ ዘንድ

• የሌሎችንም አማልክት ስም አትጥሩ

ሌሎችን አማልክት ስም መጥራት ፀሎትን የሚመለከት ነውና “ወደ ሌሎች አማልክት አትጸልዩ”

Exodus 23:14

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• በአቢብ ወር

የአቢብ ወር ለእብራውያን የአመቱ መጀመሪያ ወር ነው። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር አቢብ ወር የሚጀምረው ከመጋቢት መጨረሻ ሳምንት እስከ ሚያዝያ መጀመሪያ ሳምንት ድረስ ነው። (ዘጸአት 13፡4 ተመልከት)

• በፊቴም ባዶ እጃችሁን አትታዩ

ይህ አነጋገር እግዚአብሔር ማንም ሰው ወደ ፊቱ ሲመጣ የሆነ ነገር ተሸክሞ እንድመጣ የሚጠይቅ ይመስላል። ነገር ግን ይህ ወካይ ዘይቤ የሚያሳየው “ወደ እኔ የሚመጣ ማንም ቢሆን መስዋዕት ሳይዝ አይምጣ” ወይም “ወደ እኔ የሚመጣ ማንም ቢሆን መስዋዕት ማምጣት አለበት” የሚል ነው።

Exodus 23:16

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• የመክተቻውን በዓል ጠብቅ

ይህ በዓል የዳስ በመባል ይታወቃል። ይህ ልምምድ የመጣው እርሻቸውን በዳስ ወይም በጊዜያዊ ጎጆ ውስጥ ሆነው ያረሱና እህሉ እስኪደርስ ድረስ በዚያ ዳስ ሆነው ከአውሬ ሲጠብቁ የነበሩ አርሶ አደሮች ልምምድ ነው። “መክተቻ” የተባለው የእህል ማከማቻ ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “በዓመቱ መጨረሻ የዳስ በዓል አክብሩ”

• ወንድ ሁሉ በጌታ በእግዚአብሔር ፊት ይታይ

እዚህ ቦታ “ይታይ” የሚለው ለአምልኮ መሰብሰብን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ወንድ ሁሉ እግዚአብሔርን (ያህዌን) ለማምለክ በአንድ ላይ መሰብሰብ አለበት።

Exodus 23:18

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• የበዓሌም ስብ እስኪነጋ አይደር

ስቡ የሚበላ ሳይሆን ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መስዋዕት ሆኖ መቅረብ አለበት። ስለሆነም “ለነገ እንዲያድር አይፈቀድም ወይም እስከ ነገ መቆየት የለበትም”

• የተመረጠውን

ከእርሻ ምርቱ የተሻለውን ወይም መጀመሪያ የደረሰውን”

• ጠቦትን በእናቱ ወተት አትቀቅል

ይህ ድርጊት የከነዓናውያን ልምምድ ሲሆን ምርታማነትን ይጭምራል ተብሎ ስለሚታሰብ የሚደረግ ነው። ስለሆነም እስራኤላውያን ይህንን ድርጊት እንዳያደርጉ ተከልክለዋል። አማራጭ ትርጉም፦ “የበግ ወይም የፍየል ግልገል በእናቱ ወተት አትቀቅል”

Exodus 23:20

አጠቃላይ ዕይታ፡

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• በፊቱ ተጠንቀቁ

በጥንቃቄ ተከተለው ወይም አዳምጠህ እግዚአብሔርን (ያህዌን) ታዘዝ

• አታስመርሩ

እርሱን የምታስመርር (ለቁጣ የምታነሳሳ) ከሆነ ይቅር አይልህም

• ስሜም በእርሱ ስለ ሆነ

በዚህ ቦታ “ስም” የእግዚአብሔርን ስልጣንን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ለእርሱ ስልጣን ስለሰጠሁ

• አንተ ግን ቃሉን ብትሰማ

እግዚአብሔር (ያህዌ) የሚናገረውን በጥንቃቄ ብታደምጥ

• ጠላቶችህን እጣላቸዋለሁ፥ የሚያስጨንቁህንም አስጨንቃቸዋልሁ (ተነጻጻሪ ዘይቤ)

እንዚህ ሁለት ነገሮች ተመሳሳይ ነገር የሚገልጹና አጽንኦት ለመስጠት የገቡ ናቸው።

Exodus 23:23

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• እንደ ሥራቸውም አትሥራ

እስራኤላውያን ጣኦትን እንደምያመልኩ እንደ ሌሎች ህዝቦች መኖር የለባቸውም። አማራጭ ትርጉም፦ የሌሎችን ህዝቦች ሃይማኖታዊ ልማዶቻቸውን ወይም ሥርዓታቸውን አትከተል

• እርሱም እህልህንና ውኃህን ይባርካል (ጠቅላይ ዘይቤ)

ይህ አባባል አጠቃላይ የኑሮ ሁኔታ ለውጥ የሚመለከት ነው። ዘማራጭ ትርጉም፦ እርሱ የምትበላውን እህል እና የምትጠጣውን ውሃ ይባርክልሃል ወይም የምትበላውን እህልና የምትጠጣውን ውሃ ይባርክሃል

Exodus 23:26

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• በምድርህም መካን ወይም የምትጨነግፍ አትሆንም

በሌላ አገላለጽ፦ በምድርህ ጽንስ የሚያስወርዳት ወይም መካን ሴት አትኖርም ወይም በምድርህ ያሉ ሴቶች ያረግዛሉ እንዲሁም ይወልዳሉ

• የምትጨነግፍ

ጊዜው ሳይደርስ የምትወልድ እና ልጇ የሚሞትባት ሴት

• በፊትህም ተርብ እሰድዳለሁ

“ተርብ” ሰዎችን በመንደፍ ስቃይ የሚያስከትሉ በራሪ ነፍሳት

• ምድር ባድማ እንዳትሆን

ምድርቱ ሰው የማይኖርባት ምድር እንዳትሆን

Exodus 23:30

አጠቃላይ ዕይታ፡-

እግዚአብሔር (ያህዌ) ህጉን በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን መናገሩን ሲቀጥል እናያለን

• ወጥመድ ይሆኑብሃልና (ዘይቤያዊ አነጋገር)

“ወጥመድ” ሰዎች አውሬዎችን፥ ወፎችን፥ እና ሌሎች ነገሮችን ለማጥመድ ወይም ለመያዝ የሚጠቀሙት መሳሪያ ነው። በተመሳሳይ መልኩ እስራኤላውያን ሌሎች አማልክትን ብያመልኩ ወደ ጥፋት እንደምወስዳቸው ያመለክታል።


Chapter 24

1 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ “አንተ፣ ናዳብ፣ አብድዩና ሰባው የእስራኤል ሽማግሌዎች ወደ እኔ ኑ፤ በርቀት ሆናችሁም ስገዱልኝ። 2 ሙሴ ብቻ ወደ እኔ መቅረብ ይችላል። ሌሎች መቅረብ የለባቸውም፤ ወይም ሕዝቡ ከሙሴ ጋር መምጣት አይችሉም።” 3 ሙሴ ወደ ሕዝቡ ሄዶ እግዚአብሔር የተናገራቸውን ቃሎችና ሕጎቹን ሁሉ ነገራቸው። ሕዝቡም ሁሉ በአንድ ድምፅ፣ “እግዚአብሔር የተናገራቸውን ቃሎች ሁሉ እናደርጋለን” ብለው መለሱ። 4 ሙሴም የእግዚአብሔርን ቃሎች ሁሉ ጻፈ። ማለዳ ላይም በተራራው ግርጌ መሠዊያ ሠራ፤ ዐሥራ ሁለቱን የእስራኤል ነገዶች እንዲወክሉም፣ ዐሥራ ሁለት የድንጋይ ዐምዶችን አቆመ። 5 የሚቃጠልና የኅብረት መሥዋዕቶችን ከበሬዎች ለእግዚአብሔር እንዲያቀርቡም፣ ጥቂት የእስራኤል ወጣት ወንዶችን ላከ። 6 ሙሴ የደሙን እኩሌታ በሣህን አደረገው፣ የቀረውንም እኩሌታ በመሠዊያው ላይ ረጨው። 7 መጽሐፍ ወስዶ ለሕዝቡ ጮኽ ብሎ አነበበላቸው። ሕዝቡም፣ “እግዚአብሔር የተናገረውን ሁሉእናደርጋለን፤ እንታዘዛለንም” ብለው ተናገር። 8 ሙሴ ደሙን ወስዶ በሕዝቡ ላይ ረጨው። “ይህ፣ ይህን የተስፋ ቃል ከእነዚህ ቃሎች ጋር ለእናንተ በመስጠት፣ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር የገባው የኪዳኑ ደም ነው” በማለትም ተናገረ። 9 ከዚያም በኋላ ሙሴ፣ አሮን፣ ናዳብ፣ አብድዩና ሰባው የእስራኤል ሽማግሌዎች ወደ ተራራው ወጡ። 10 የእስራኤልን አምላክ አዩት። ከእግሮቹ ሥርም እንደ ንጹሕ ሰማይ ከጠራ የሰንፒር ድንጋይ የተሠራ ወለል ነበረ። 11 በእስራኤላውያን ሽማግሌዎች ላይ ተቆጥሮ እጅ አላሳረፈባቸውም። እነርሱ እግዚአብሔርን አዩ፤ በሉ፣ ጠጡም። 12 እግዚአብሔር ሙሴን፣ “ተራራው ላይ ወደ እኔ ና፤ በዚያም ቆይ። የድንጋይ ጽላቱን ሕዝቡን እንድታስተምራቸውም የፋጽሏቸውን ሕጉንና ትእዛዛቱን እሰጥሃለሁ” አለው። 13 ስለዚህ ሙሴ ከረዳቱ ከኢያሱ ጋር ወደ እግዚአብሔር ተራራ ሄደ። 14 ሙሴ ሽማግሌዎቹን፣ “ተመልሰን ወደ እናንተ እስክንመጣ ድረስ እዚህ ቆዩን። አሮንና ሖር ከእናንተ ጋር ናቸው። ክርክር የሚኖርበት ሰው ካለ፣ ወደ እነርሱ ይቅረብ” አላቸው። 15 ወደ ተራራው ወጣ፤ ደመናውም ተራራውን ሸፈነው። 16 የእግዚአብሔር ክብር በሲና ተራራ ላይ ወረደ፤ ደመናውም ተራራውን ስድስት ቀን ሸፈነው። በሰባተኛው ቀን እግዚአብሔር ከደመናው ውስጥ ሙሴን ጠራው። 17 የእግዚአብሔርን ክብር እስራኤላውያን ሲያዩት እንደሚያጋይ እሳት ነበር። 18 ሙሴ ደመናው ውስጥ ገብቶ ወደ ተራራው ወጣ። በተራራውም ላይ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ቆየ።



Exodus 24:1

• ናዳብም አብዩድም

እነዚህ የወንዶች ስም ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ ስሞችን የመተርግሞ ዘዴ የሚለውን ተመልከት፤ ከዘጸአት 6፡23 ጋር አነጻጽር።

• ከእስራኤልም ሰባ ሽማግሌዎች

ከእስራኤል ሰዎች ወይም መሪዎች ሰባ የሚሆኑ

Exodus 24:3

• በአንድ ድምፅ

ይህ ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን ህዝቡ በፍጹም መስማማት መሆናቸውን ያሳያል። አማራጭ ትርጉም፦ በአንድነት ወይም በመስማማት

• ከተራራውም በታች

በተራራው ሥር ወይም ከተራራው ግርጌ ማለት ነው

Exodus 24:5

• የደሙን እኵሌታ ወስዶ በቆሬ ውስጥ አደረገው

ሙሴ ሰዎችን ለመርጨት ከደሙ ግማሹን ወስዶ በገበቴ ወይም በባዝ ውስጥ አኖረው። ይህ የሚያሳየው የእስራኤል ህዝብ ከእግዚአብሔር ጋር ለሚያደርገው ቃል ኪዳን ማጽኛ ይሆን ዘንድ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “ሙሴም ከእንስሶቹ ደም ግማሹን ወስዶ በገበቴ ውስጥ አኖረው”

• የደሙንም እኵሌታ በመሠዊያው ረጨው

“መሰዊያው” እግዚአብሔርን የሚወክል ነው። ይህ የሚያሳየው እግዚአብሔር በቃል ኪዳን ተሳታፊ መሆኑ የሚያረጋግጥ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “ከእንስሳው ደም ግማሹን በመሠዊያው ፊት ረጨው”

Exodus 24:7

• እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን

በሌላ አገላለጽ፦ ለእግዚአብሔር በሁሉ ነገር እንታዘዛለን

• ሙሴም ደሙን ውስዶ

ይህ ደም ሙሴ በገበቴው ውስጥ የጨመረው ደም እንጂ ሌላ ደም አይደለም። አማራጭ ትርጉም፦ “ሙሴ በገበቴ ያለውን ደም ወስዶ

Exodus 24:9

• ናዳብም አብዩድም

እነዚህ የወንዶች ስም ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ ስሞችን የመተርግሞ ዘዴ የሚለውን ተመልከት፤ ከዘጸአት 6፡23 ጋር አነጻጽር።

• ከእግሩም በታች

ይህ አባባል እግዚአብሔር እግር እንዳለው አድርጎ የሚያቀርብ ሰውኛ ዘይቤ ነው።

• እንደ ሰማይ መልክ የሚያበራ እንደ ብሩህ ሰንፔር ድንጋይ የሚመስል ወለል

ሰንፔር ከሚመባል ከሰማያዊ ድንጋይ የተሰራ የሚያንጸባርቅ ወለል

• ወለል

ጠንካራ የሆነ ለመራመድ ወይም ለመንዳት የሚያገልግል

• እንደ ሰማይ መልክ

ሰማያዊ ቀለም ያለው (የማይታወቁ ነገሮችን የመተርጎም ዘዴ የሚለውን ተመልከት)

• ሰንፔር ድንጋይ

የከበረ (ውድ) ድንጋይ ሲሆን ቀለሙ ሰማያዊ ነው

• እንደ ሰማይ መልክ የሚያበራ

ይህ ተነጻጻሪ ዘይቤ ሲሆን “እንደ ጠራ ሰማይ የሚያበራ ወይም ደመና እንደሌለው ሰማይ የጠራ”

• እጁንም በእስራኤል አዛውንቶች ላይ አልዘረጋም

ይህ ማለት እግዚአብሔር የእስራኤል ሽማግሌዎችን አልጎዳቸውም ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር የእስራኤል መሪዎች የሆኑ ሰዎችን አልቀሠፈም”

Exodus 24:12

• ሕግና ትእዛዝ የድንጋይም ጽላት እሰጥሃለሁ

በጠፍጣፋ ድንጋዮች ላይ እግዚአብሔር ህጉንና ትዕዛዛቱን ጻፌ። በሌላ አባባል፦ “እኔ በእነርሱ ላይ ትዕዛዛቱን የጻፍኩባቸውን ሁለቱን የድንጋይ ጽላቶች”

• ሙሴና ሎሌው ኢያሱ ተነሡ

ሙሴ ከረዳቱ ወይም ከአገልጋዩ ኢያሱ ጋር ተነሱ

Exodus 24:14

• በዚህ ቆዩን

እኔንና ኢያሱን ጠብቁ

• ሖር

ይህ ሰው የሙሴና የአሮን ቅርብ ጓደኛቸው ነው፤ ዘጸአት 17፡10 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት

Exodus 24:16

• የእግዚአብሔርም ክብር

የእግዚአብሔርን ህልዎት የሚወክለው አንጸባራቂ ብርሃን

• እንደሚያቃጥል እሳት ነበረ (ተነጻጻሪ ዘይቤ)

የእግዚአብሔር (የያህዌ) ክብር ትልቅና እንደ እሳት የሚያቃጥል ሆኖ ቀርቧል። አማራጭ ትርጉም፦ እንደ ትልቅ እሳት የሚያቃጥል ነበር

• በእስራኤል ልጆች ፊት

ዓይኖቻቸው ማየትን፥ ማየታቸው ደግም ሀሳባቸውን ወይም የሚያዩትን ነገር እንዴት እንደሚፈርጁ አመልካቺ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ በእስራኤል ሕዝብ ዘንድ


Chapter 25

1 ሙሴን እንዲህ አለው፤ 2 “እያንዳንዱ ሰው ልቡ በፈቀደለት መሠረት ስጦታ ለእኔ እንዲያመጣ ለእስራኤላውያን ንገር። እነዚህን ስጦታዎች ተቀበልልኝ። 3 ከእነርሱ የምትቀበላቸውም ስጦታዎች እነዚህ ናቸው፦ ወርቅ፣ ብርና ነሐስ፤ 4 ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና የበፍታ ድር ልብስ፣ የፍየል ጠጕር፣ 5 ቀለም የተነከረ የአውራ በግ ቆዳና የአቆስጣ ቁርበት፣ የግራር ዕንጨት፤ 6 ለመቅደሱ መብራቶች ዘይት፣ ለመቅቢያው ዘይት ቅመሞችና ጣፋጭ መዐዛ ያለው ዕጣን፤ 7 ለኤፉድና ለደረት ኪሱ የሚሆኑ መረግዶችና ሌሎች ዕንቆች። 8 እንዳድር ሕዝቡ መቅደስ ይሥሩልኝ። 9 ለመገናኛው ድንኳንና ለዕቃዎቹ ሁሉ እኔ ባሳየሁህ ምሳሌ መሠረት ሥሩት። 10 ሁለት ክንድ ተኩል፣ ስፋቱ አንድ ክንድ ተኩል፣ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ ታቦት ከግራር ዕንጨት ይሠሩ። 11 ውስጡንም ውጭውንም በንጹሕ ወርቅ ለብጠው፤ በዙሪያውም የወርቅ ክፈፍ አድርግለት። 12 የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተህለት በታቦቱ አራት እግሮች ላይ፣ ሁለቱን በአንድ ጎኑ፣ ሁለቱን ደግሞ በሌላው ጎኑ አስቀምጣቸው። 13 መሎጎያዎችን ከግራር ዕንጨት ሥራና አወርቅ ለብጣቸው። 14 ታቦቱን ለመሸከም መሎጊያዎቹን በታቦቱ ጎን ባሉ ቀለበቶች ውስጥ አስገባ። 15 መሎጊያዎቹ ምንጊዜም በታቦቱ ቀለበቶች ውስጥ ይቀመጣሉ እንጂ ከዚያ አይወጡም። 16 የኪዳኑን ምስክሮች በታቦቱ ውስጥ ታስቀምጣለህ። 17 ሁለት ክንድ ተኩል፣ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ከንጹሕ ወርቅ ሥራ። 18 ለሁለቱ የስርየት መክደኛ ጫፎች ሁለት ኪሩቤልን ከተቀጠቀጠ ወርቅ ትሠራለህ። 19 ኪሩብ ለስርየት መክደኛው አንድ ጫፍ፣ ሌላውን ኪሩብ ደግሞ ለሌላው ጫፍ በማድረግ ከስርየት መክደኛው ጋር ወጥ ሆነው መሠራት አለባቸው። 20 ክንፎቻቸውን ወደ ላይ መዘርጋትና የስርየት መክደኛውን በክንፎቻቸው መጋረድ ይኖርባቸዋል። እርስ በርሳቸው መተያየትና ወደ ስርየት መክደኛውም መመልከት አለባቸው። 21 መክደኛውን በታቦቱ ላይ ታደርገዋለህ፤ በታቦቱ ውስጥም የምሰጥህን የኪዳኑን ምስክሮች ታስቀምጣለህ። 22 እኔ ከአንተ ጋር የምገናኘው በታቦቱ ነው። በስርየት መክደኛው ላይ ሆኜ ከአንተ በተናገርሁበት በምስክሩ ታቦት ላይ ባሉት በሁለቱ ኪሩቤል መካከል ነው። 23 እርዝመቱ ሁለት ክንድ፣ ወርዱ አንድ ክንድ፣ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ ጠረጴዛ ከግራር ዕንጨት ሥራ። 24 ወርቅ ለብጠው፤ በዙሪያውም የወርቅ ክፈፍ አድርግለት። 25 አንድ ስንዝር ስፋት ያለው ጠርዝ ለጠርዙ በዙሪያው ከሚኖረው የወርቅ ክፈፍ ጋር አብጅለት። 26 አራት የወርቅ ቀለበቶችን ሥራለትና ቀለበቶችን አራቱ እግሮቹ ባሉበት ከሚገኙት አራት ማዕዘኖች ጋር አያይዛቸው። 27 ለማስቀመጥና ጠረጴዛውን መሸከም እንዲቻል፣ ቀለበቶቹ ከክፈፉ ጋር መያያዝ አለባቸው። 28 የጠረጴዛው መሸከሚያ እንዲሆኑም መሎጊያዎችን ከግራር ዕንጨት ሥራና በወርቅ ለብጣቸው። 29 ቊርባኑን ለማፍሰስ ጥቅም እንዲሰጡ ወጭቶችን፣ ጭልፋዎችን፣ ማንቆርቆሪያዎችንና ጎድጓዳ ሣህኖችን ከንጹህ ወርቅ ሥራ። 30 በጠረጴዛውም ላይ የገጽ ኅብስት ሁልጊዜ በፊቴ ታደርጋለህ። 31 መቆሚያና ዘንግ አበጅተህበት ከተቀጠቀጠ ንጹሕ ወርቅ መቅረዝ። ጽዋዎቹ፣ ቀንበጦቹና አበባዎቹ ሁሉ ወጥ ሆነው ከመቅረዙ ጋር ይሠራሉ። 32 ሦስት ቅርንጫፎች በአንድ ጎን፣ ሦስት ቅርንጫፍ ደግሞ በሌላው ጎን፣ ስድስት ቅርንጫፎች ለመቅረዙ ይውጡለት። 33 የመጀመሪያው ቅርንጫፍ የለውዝ አበቦችን መስለው የተሠሩ ሦስት ጽዋዎች ከቀንበጥና ክአበባ ጋር፣ በሌላው ቅርንጫፍም እንደዚሁ የለውዝ አበቦችን የሚመስሉ ሦስት ጽዋዎች የተቀረጹበት ከቀንበጥና ከአበባ ጋር ሊኖሩት ይገባል። ከመቅረዙ በሚወጡት በስድስት ቅርንጫፎች ሁሉ ላይ የሚሆነውም እንደዚሁ አንድ ዐይነት ነው። 34 ላይ የለውዝ አበባ መስለው የተቀረጹ አራት ጽዋዎች ከቀንበጦቹና ከአበባዎቹ ጋር ሊኖሩበት ይገባል። 35 በመጀመሪያዎቹ ቅርንጫፎች ጥንድ ሥር ወጥ ሆኖ ዐብሮ የተሠራ ቀንበጥ፣ በሁለተኛው የቅርንጫፎች ጥንድ ሥርም እንደዚሁ ወጥ ሆኖ ዐብሮ የተሠራ ቀንበጥ ይኖረዋል። በሦስተኛው የቅርንጫፎቹ ጥንድ ሥርም ወጥ ሆኖ ዐብሮ የተሠራ ቀንበጥ ይበጅለታል። ከመቅረዙ በሚወጡ በስድስቱ ቅርንጫፎች ሁሉ የሚሆነውም ይኸው አንድ ዐይነት ነው። 36 ቀንበጦቻቸውና ቅርንጫፎቻቸው ሁሉ አንድ ወጥና ከተቀጠቀጠ ንጹሕ ወርቅ የተሠሩ መሆን አለባቸው። 37 መቅረዙንና ሰባት መብራቶችን ሠርተህ ፊት ለፊት ላለው ስፍራ ብርሃን እንዲሰጥ አድርግ። 38 የኵስታሪ መሰብሰቢያ ሣህኖቻቸው ከንጹሕ ወርቅ መሠራት አለባቸው። 39 መቅረዙንና የመቅረዙን ዕቃ ሁሉ ለመሥራት አንድ መክሊት ንጹሕ ወርቅ ተጠቀም። 40 ላይ ባሳየሁህ ምሳሌ መሠረት የሠራሃቸው ስለ መሆንህ እርግጠኛ ሁን።



Exodus 25:1

• በልቡ ከሚያምረው ሰው ሁሉ

ይህ ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን ስጦታ ለመስጠት የተነሳሳን አንድ ሰው ፍልጎት ወይም በጎ ፈቃድ ያሳያል አማራጭ ትርጉም፦ ስጦታ ለመስጠት የሚፈልግ ሰው

• መባ ተቀበሉ

“ተቀበሉ” ተብሎ የተነገራቸው ሙሴንና የእስራኤል መሪዎችን/ሽማግሌዎችን/ ነው። የሚቀበሉትም ህዝቡ የሚያመጣውን ስጦታ ወይም መስዋዕት ወይም ቁርባን ነው።

Exodus 25:3

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ማድረግ ያለባቸውን ነገር እግዚአብሔር(ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• ሰማያዊ፥ ሐምራዊና ቀይ ግምጃ

አማራጭ ትርጉሞች፦ 1) በሰማያዊ፥ ሀምራዊና ቀይ ቀለም የተቀቡ ልብሶች/ሶፎች/ ወይም 2) ላይነኖችን ለመቀባት የሚረዱ ሰማያዊ፥ ሐምራዊና ሰማያዊ ቀለም

• ቀይ ግምጃ

ነጣ ያለ ቀይ ቀለም ወይም በቀይ ቀለም የተቀለመ ጨርቅ

• የአስቆጣ ቁርበት

ግዙፍና ሳር በል የሆነ የባህር እንስሳ

• ለጣፋጭ ዕጣን ቅመም

የደረቁ የእጽዋት ተዋጽኦ ሲሆን ሰዎች ፈጭተው ጥሩ ሽታ እንድኖረው ዘይት ወይም ምግብ በዚያ ላይ ጨምረው የሚሰሩት ነው።

• መረግድ

በላዩ ላይ ሁለት ቅርፍት ያለው ማለትም ነጭ ወይም ጥቁር፥ ቀይ ያለው የድንጋይ ዓይነት

Exodus 25:8

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ቤተ መቅደስ . . . ድንኳን

“ቤተ መቅደስ” የሚለው “ቅዱስ ስፍራ” የሚገልጽ ሲሆን “ድንኳን” ደግሞ “ቅዱስ ድንኳን” ወይም ጊዜያዊ ቤት/መቆያ/ዳስ/ የሚል ፍቺ አለው። ሁለቱም ተመሳሳይ ፍቺ የሚሰጡ ተወራራሽ ቃላት ናቸው።

• እኔ እንደማሳይህ ሁሉ . . . እንዲሁ ሥሩት

“እኔ በማሳይህ” የሚለው ሀረግ ሙሴን የሚመለከት ሲሆን “ሥሩት” ሙሴንና የእስራኤልን ህዝብ የሚመለከት ነው።

• እኔ እንደማሳይህ ሁሉ

ሁሉንም እኔ በማሳይህ ዕቅድ መሠረት

Exodus 25:10

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፤ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል

ርዝመቱ አንድ ሜትር ከአስራ አምስት ሴንቲ ሜትር ስፋቱና ከፍታው ሥልሳ ዘጠኝ ሳንቲ ሜትር። አንድ ክንድ 46 ሴንቲ ሜትር ያክል ነው።

Exodus 25:12

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• አራት የወርቅ ቀለበቶችም አድርግለት

“የወርቅ ቀለበቶችን አድርግለት” የሚለው ወርቆችን በማቅለጥ በቀለበት መልክ ማውጣቱን ወይም ማድረቁን የሚመለከት ነው። በሌላ አገላለጽ፦ አራት የወርቅ ዋልታዎችንም ወይም ቀለበቶችን ሠርተህ

• ለታቦቱ መሸከሚያ

ታቦቱን ለመሸከም እንዲያገለግል

Exodus 25:15

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የስርየት መክደኛ

በምስክሩ ታቦት ላይ የሚቀመጥና የስርየት መስዋዕቱን የሚሸፍን መክደኛ ነው

• ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፤ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል

ርዝመቱ አንድ ሜትር ከአስራ አምስት ሴንቲ ሜትር ስፋቱና ከፍታው ሥልሳ ዘጠኝ ሳንቲ ሜትር። አንድ ክንድ 46 ሴንቲ ሜትር ያክል ነው።

• የተቀጠቀጠ ወርቅ

ተቀጥቅጦ የተሰራ ወርቅ

Exodus 25:19

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የስርየት መክደኛ

በምስክሩ ታቦት ላይ የሚቀመጥና የስርየት መስዋዕቱን የሚሸፍን መክደኛ ነው

• በአንድ ላይ ትሠራዋለህ

እነርሱም ከክዳኑ ጋር አብረው/ተያይዘው/ የተሠሩ ይሁኑ

Exodus 25:22

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል

• በዚያም ከአንተ ጋር እገናኛለሁ

እኔ በታቦቱ መክደኛ ላይ ባሉ በሁለቱ ክሩቤሎች ውስጥ ሆኜ ለአንተ እገለጥልሃለሁ

• የስርየት መክደኛ

በምስክሩ ታቦት ላይ የሚቀመጥና የስርየት መስዋዕቱን የሚሸፍን መክደኛ ነው

Exodus 25:23

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፤ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል

ርዝመቱ አንድ ሜትር ከአስራ አምስት ሴንቲ ሜትር ስፋቱና ከፍታው ሥልሳ ዘጠኝ ሳንቲ ሜትር። አንድ ክንድ 46 ሴንቲ ሜትር ያክል ነው።

Exodus 25:25

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• አንድ ጋት የሚያህል ክፈፍ

በባህላዊው ልከት አንድ ጋት የአራት ጣቶች ጥምር ማለት ሲሆን ከ8-10 ሳንቲ ሜትር ያህል ነው።

• ክፈፍ አድርግለት

ጠርዝ ሥራለት/አብጅለት/

• የወርቅ ቀለበቶች አድርግለት

የወርቅ ቀለበቶችን በጠርዙ ላይ አያይዝ

• ገበታውንም ለመሸከም

ጠረጴዛውን ለመሸከም እንዲያገለግል

Exodus 25:28

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ገበታውን ይሸከሙባቸው ዘንድ

በሌላ አገላለጽ፦ አንተ እነርሱን አስገብተህ ጠረጴዛውን መሸከም እንድትችል

• ለማፍሰሻም ይሆኑ ዘንድ

በሌላ አገላለጽ፦ አንተ እነርሱን ለወይን ጠጅ መቅጃ እንድትጠቀም

• በገበታም ላይ የገጽ ኅብስት

በጠረጴዛው ላይ ሆኖ ለእኔ የሚቀርበው የተቀደሰ ኅብስት/ዳቦ/

Exodus 25:31

• መቅረዝንም ከጥሩ ወርቅ አድርግ

መብራት ማስቀመጫ ባላ መሳይ ነገር

• ጽዋዎቹም ጕብጕቦቹም አበቦቹም አንድነት በእርሱ ይደረጉበት

ለጌጥ ወይም የውበት አበባዎች፥ እንቡጦችና ቀንበጦች ከእርሱ ጋር አንድ ሆነው ይሠሩ

Exodus 25:33

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል። በሚቀጥሉት ክፍሎች እግዚአብሔር (ያህዌ) የመብራት ማስቀመጫውን (የመቅረዙን) አሰራር ዝርዝር ይናገራል (ዘጸአት 25፡31-32 ተመልከት)

• የለውዝ አበባ የሚመስሉትን ጽዋዎች

ነጭ ወይም ሮዝ ቀለም/ቀላ ያለ አምራዊ/ መልክ ያለው አበባ የሚያወጣና አምስት ቀነበጦች ያሉት

Exodus 25:35

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል። በሚቀጥሉት ክፍሎች እግዚአብሔር (ያህዌ) የመብራት ማስቀመጫውን (የመቅረዙን) አሰራር ዝርዝር ይናገራል (ዘጸአት 25፡31-32 ተመልከት)

• ጕብጕቦቹና ቅርንጫፎቹ ሁሉ ከእርሱ ጋር አንድ ይሁኑ

እንቡጦቹ፥ ቅርንጫፎቹና መቅረዙ ሁሉም አንድ ወጥ ሆነው ይሰሩ

Exodus 25:37

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• በፊቱ ያበሩ ዘንድ

ከፊት ለፊት በኩል ወይም ወደ ፊት እንዲያበሩ

• መኮስተሪያዎችዋን የኩስታሪ ማድረጊያዎችዋንም ከጥሩ ወርቅ አድርግ

መለኮሻዎችንና የአመድ ማስቀመጫ ሳሕኖችን ከንጹሕ ወርቅ ሥራ

• መቅረዙም ዕቃውም ሁሉ ከአንድ መክሊት ጥሩ ወርቅ ይሠሩ

አንድ መክሊት ወደ ከ33-35 ኪሎ ግራም ያህል ነው። በሌላ አገላለጽ፦ መብራት ማስቀመጫውን (መቅረዙን) እና እነዚህን ሁሉ ዕቃዎች ሠላሳ አምስት ኪሎ ግራም ከሆነ ንጹሕ ወርቅ ሥራ።

• በተራራ ላይ እንዳሳየሁህ ምሳሌ እንድትሠራ ተጠንቀቅ

አማራጭ ትርጉም፦ “እኔ አንተን በተራራው ላይ ያሳየሁትን ምሳሌ ተከትለህ በጥንቃቄ ሥራ”


Chapter 26

1 ከተፈተለ በፍታ ድር፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ ከተሠሩና ኪሩቤል ከተጠለፉባቸው ዐሥር መጋረጃዎች ጋር ማደሪያ ድንኳኑን ሥራ። ይህም ብልኅ ሠራተኛ የሚሠራው ሥራ ነው። 2 የያንዳንዱ መጋረሣ እርዝመት ሃያ ስምንት ክንድ፣ ወርዱ አራት ክንድ ይሁን። መጋረጃዎቹ ሁሉ እኩል መጠን ይኑራቸው። 3 ዐምስቱ መጋረጃዎች እርስ በርስ መያያዝ አለባቸው፤ ሌሎቹ ዐምስት መጋረጃዎችም እንደዚሁ እርስ በርሳቸው መገጣጠም ይኖርባቸዋል። 4 በአንደኛው ወገን የመጨረሻ መጋረጃ የውጭ ጠርዝ ላይ የሰማያዊ ግምጃ ቀለበቶችን አድርግ። ለሁለተኛው ወገን የመጨረሻ መጋረጃ የውጭ ጠርዝም ይህንኑ አበጅለት። 5 ዐምሳ ቀለበቶችን በአንደኛው የመጋረጃ ወገን፣ ዐምሳ ቀለበቶችን በሌላው የመጨረሻ መጋረጃ ላይ አድርግ። ይህን የምትሠራውም ቀለበቶቹ እርስ በርስ እንዲተያዩ በማድረግ ነው። 6 ዐምሳ የወርቅ ማያያዣዊችብ ሠርተህ ማደሪያ ድንኳኑ አንድ እንዲሆን፣ መጋረጃዎቹን በእነርሱ አያይዛቸው። 7 ከማደሪያው በላይ ለድንኳን የሚሆኑ ዐሥራ አንድ የፍየል ጠጕር መጋረጃዎችን ሥራ። 8 መጋረጃ እርዝመት ሠላሳ ክንድ፣ ወርዱ አራት ክንድ ይሁን። ዐሥራ አንዱም መጋረጃዎች እኩል መጠን ይኑራቸው። 9 ዐምስት መጋረጃዎችን በአንድነት፣ ስድስት መጋረጃውችንም እንዲሁ እርስ በርስ አያይዛቸው። ስድስተኛውን መጋረጃ በድንኳኑ ፊት ዕጠፈው። 10 በመጀመሪያ ተገጣጣሚ የመጨረሻ መጋረጃ ጠርዝ ላይ ዐምሳ ቀለበቶችን፣ ሁለተኛውን የመጋረጃ አካል በሚያገጣጥመው የመጨረሻ መጋረጃ ጠርዝ ላይም እንደዚሁ ዐምሳ ቀለበቶችን አድርግ። 11 ዐምሳ የነሐስ ማያያዣዎችን ሥራና በቀለበቶቹ ውስጥ አስገ ባቸው። ከዚያም አንድ ወጥ እንዲሆን ድንኳኑን አገጣጥመው። 12 መጋረጃዎች ተንጠልጥሎ ያለው ቀሪ ግማሽ መጋረጃ ከማደሪያ ድንኳኑ ጀርባ ይንጠልጠል። 13 ከመጋረጃዎቹ እርዝመት የተረፈው በአንድ በኩል አንድ ክንድ ምጋረጃ፣ 14 በሌላው ጎንም አንድ ክንድ መጋረጃ ማደሪያው ድንኳን መሸፈኛ በቀይ ቀለም የተነከረ የአውራ በግ ቆዳና ከዚያም በላይ የሚሆን የአስቆጣ ቁርበት አዘጋጅ። 15 ለማደሪያው ድንኳን የሚሆኑ ወጋግራዎችን ከግራር ዕንጨት አብጅ። 16 ወጋግራ እርዝመት ዐሥር ክንድ፣ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል ይሁን። 17 በርስ የሚያገናኗቸው ሁለት ጕጣጕጦች በያንዳንዱ ወጋግራ ላይ ይኑር። የመገናኛ ድንኳኑን ወጋግራዎች ሁሉ በዚህ መንገድ ሥራ። 18 ድንኳን ወጋግራዎችን ስታበጅ፣ በደቡብ መኩል ላለው ሃያ ወጋግራዎችን አብጅ። 19 ወጋግራዎች የሚሆኑ አርባ የብር መቆሚያዎችን አብጅ። ከመጀመሪያው ወጋግራ ሥር ሁለት መጋጠሚያዎች እንዲሆኑ ሁለት መቆሚያዎች ይኑሩ። በሌሎች ወጋግራዎች በያንዳንዳቸው ሥርም ለሁለት መጋጠሚያዎቻቸው ሁለት መቆሚያዎች ይዘጋጁ። 20 በሰሜን በኩል ላለው ለሁለተኛው የመገናኛው ድንኳን ጎን ሃያ ወጋግራዎችንና አርባ የብር መቆሚያዎቻቸውን ሥራ። 21 በመጀመሪያው ወጋግራ ሥር ሁለት መቆሚያዎች፣ በሚቀጥለው ወጋግራ ሥርም እንደዚሁ ሁለት መቆሚያዎች. በእያንዳንዱ ሥር ይሁኑ። 22 በምዕራብ በኩል ላለው ለመገናኛው ድንኳኑ የኋላ ጎን ስድስት ወጋግራዎችን አብጅ። 23 ለኋላ ማእዘኖቹም ሁለት ወጋግራዎችን አብጅ። 24 እነዚህ ወጋግራዎች ከታች ጥንድ፣ ከላይ ደግሞ በአንድ ቀለበት የተያያዙ መሆን አለባቸው። ለሁለቱም የኋላ ማእዘኖች የሚሆነው በዚህ መንገድ ነው። 25 ወጋግራዎች ከብር መቆሚያዎቻቸው ጋር ሊኖሩ ይገባል። በሁሉም ዐሥራ ስድስት መቆሚያዎች ናቸው ያሉት፤ በመጀመሪያው ወጋግራ ሥር ሁለት መቆሚያዎች፣ በሚቀጥለው ወጋራ ሥርም ሁለት መቆሚያዎችና በእያንዳንዱም ሥር እንዲሁ። 26 ድንኳኑ አንደኛ ጎን ወጋግራዎች ዐምስት አግዳሚዎችን ከግራር ዕንጨት አዘጋጅ፤ 27 ለማደሪያ ድንኳኑ ሌላ ጎንም ወጋግራዎች ዐምስት አግዳሚዎችን፣ በምዕራብ በኩል ላለው ለመገናኛ ድንኳኑ የኋላ ጎን ወጋግራዎችም ዐምስት አግዳሚዎችን እንዲሁ አብጅ። 28 በወጋግራዎቹ መካከል ላይ ያለው አግዳሚ ከዳር እስከ ዳር መድረስ አለበት። 29 ወጋግራዎቹን በወርቅ ለብጣቸው። አግዳምዎችን ደግፍ በመያዝ እንዲያገለግሉም የወርቅ ቀለበቶቻቸውን ሥራላቸው፤ አግዳሚዎችንም በወርቅ ለብጣቸው። 30 ድንኳኑን መትከል ያለብህ በተራራው ላይ ያየኸውን ምሳሌ በመተከትል ነው። 31 ብልኅ ሠራተኛ ኪሩቤልን የጠለፈበት፣ የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ግምጃና አምሮ የተፈተለ በፍታ መጋረጃ አብጅ። 32 በወርቅ በተለበጡ የግራር ዕንጨት አራት ዐምዶች ላይ ልትሰቅለው ይገባል። እነዚህ ዐምዶች በአራት የብር መቆሚያዎች ላይ የተቀመጡ የወርቅ ኵላቦች ይኖሯቸዋል። 33 መጋረጃውን በማያያዣዎቹ አንጠልጥለው፤ የምስክሩንም ታቦት አግባው። መጋረጃው ቅድስቱን ከቅድስተ ቅዱሳን ይለየዋል። 34 በቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ባለ ውበምስክሩ ታቦት ላይ የስርየት መክደኛውን አስቀምጥ። 35 ከመጋረጃው ውጭ፣ መቅረዙንም ከመገናኛው ድንኳን ደቡባዊ ጎን ከጠረጴዛው ትይዩ አስቀምጥ። ጠረጴዛው በሰሜናዊ ጎኑ በኩል መቀመጥ ይኖርበታል። 36 መግቢያ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና አምሮ ከተፈተለ በፍታ በጥልፍ ብሚያስጌጥ ሠራተኛ የተሠራ መጋረጃ አብጅለት። 37 ዐምስት ምሰሶዎችን ከግራር ዕንጨት አብጅና በወርቅ ለብጣቸው። ኵላቦቻቸውም የውርቅ መሆን እላቸው፤ ዐምስት የነሐስ መቆሚያዎችንም ሥራላቸው።



Exodus 26:1

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• ማደሪያ ሥራ

በዚህ ክፍል “ሥራ” ተብሎ የታዘዘው ሙሴ ነው። ሙሴ ሥራውን ለሚሰራው ሰው የሥራውን ዝርዝር እንዲያሳየውና በሀላፊነት እንዲቆጣጠረው መታዘዙን ያመለክታል። አማራጭ ትርጉም፦ “ለሠራተኛው ንገረው”

• መጋረጃ

ክብደት ያለው እና ትልቅ የተሰፋ ጨርቅ ሲሆን መገናኛውን ድንኳን ለመሸፈንና የድንኳኑን ውስጠኛውን ክፍል ለመከፋፈል የሚያገለግል ነው።

• ከቀይም ግምጃ የተሠሩ

በቀይ ቀለም የተቀባ ወይም የተነከረ ሱፍ ጨርቅ

• ብልህ ሠራተኛ

የተውቡና ያገጡ ነገሮችን በእጅ የሚሰራ “እደ ጥበብ” ሰራተኛ

• ርዝመት ሀያ ስምንት ክንድ፥ ወርዱም አራት ክንድ ይሁን

ርዝመቱ 12 ሜትር ከ88 ሳ.ሜት እንዲሁም ወርዱ 1.ሜትር ከ82 ሳንት ሜትር

• አምስቱ መጋረጆች እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ ይሁኑ፣ አምስቱም መጋረጆች እንዲሁ እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ ይሁኑ

በአድራጊ ግስ ሲጻፍ፦ አምስቱን መጋረጃዎችን በአንድ ላይ ስፏቸው እንዲሁም ሌሎችን አምስት መጋረጃዎችን በአንድ ሰፏቸው

Exodus 26:4

• ቀለበቶች አድርግ

መጋረጃዎችን ለማያያዝ የሚጠቅሙ/የሚያገለግሉ/ ከሰማያዊ ጨርቅ የተሰሩ ቀለበቶች ናቸው።

Exodus 26:7

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• አስራ አንድ . . . ሠላሳ . . . አራት

የመጋረጃዎችን ርዝመት፥ ስፋትና ከፍታ የሚያሳዩ ቁጥሮች ናቸው።

• ክንድ

አንድ ክንድ 46 ሴንት ሜትር ያህል ነው

Exodus 26:10

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ቀለበቶች

መጋረጃዎችን ለማያያዝ የሚጠቅሙ/የሚያገለግሉ/ ከሰማያዊ ጨርቅ የተሰሩ ቀለበቶች ናቸው

Exodus 26:12

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ክንድ

አንድ ክንድ 46 ሴንት ሜትር ያህል ነው

• ከቀይ አውራ በግ ቁርበት

በቀይ ቀለም የተነከረ የበግ ቁርበት

Exodus 26:15

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ለማደሪያውም የሚቆሙትን ሳንቆች

ድንኳኑን የሚደግፉ ቋሚዎችን ወይም ለማደሪያው ድንኳን ወጋግራዎችን አብጅ”

• አንድ ክንድ ተኩል

ወደ ሰባ (70) ሴንት ሜትር ያህል ነው

Exodus 26:19

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የብር እግሮችን አድርግ

የብር መቆሚያዎችን አብጅ

• ከእያንዳንዱም ሳንቃ በታች ሁለት እግሮች ይሁኑ

በእያንዳንዱ ወጋግራ/ተራዳ ሥር ሁለት ሁለት መቆሚያ አድርግ

Exodus 26:22

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ከታችም እስከ ላይ እስከ አንደኛው ቀለበት ድረስ አንዱ ሳንቃ ድርብ ይሁን

ከታች በኩል ተጣምረው እስከ ላይ አንደኛው ዋልታ መያያዝ አለባቸው

• የብር እግሮቻቸው ይሁኑ

የብር መቆሚያዎች ይኑሩ/ይሰሩ/

Exodus 26:26

አጠቃላይ ምልከታ፦

የመገናኛውን ድንኳን እንዴት መገንባት እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል

• መወርወሪያዎች

አግዳሚዎች/ አግዳሚ ብረቶች/አግዳሚ እንጨቶች/

• በማደሪያውም በስተ ኋላ በምዕራብ ወገን ላሉት ሳንቆች

የመገናኛው ድንኳን ፊቱ ወደ ምስራቅ የተመለሰ ነው

Exodus 26:31

አጠቃላይ ምልከታ፦

የመገናኛውን ድንኳን እንዴት መገንባት እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል

አድርግ

በዚህ ክፍል “አድርግ” ተብሎ የታዘዘው ሙሴ ነው። ሙሴ ሥራውን ለሚሰራው ሰው የሥራውን ዝርዝር እንዲያሳየውና በሀላፊነት እንዲቆጣጠረው መታዘዙን ያመለክታል። አማራጭ ትርጉም፦ “እንዲሠራ ለሠራተኛው ንገረው”

• የምስክርን ታቦት አግባው

የቃል ኪዳን ታቦት ከመጋረጃው በስተኋላ በኩል አኑረው/አስቀምጠው

• መጋረጃውም በቅድስቱና በቅድስተ ቅዱሳኑ መካከል መለያ ይሁናችሁ

መጋረጃው ቅድስት የተባለውን ስፍራ ቅድስተ ቅዱሳኑ ከተባለው ሥፍራ የሚለይ ይሁን

Exodus 26:34

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የስርየት መክደኛውን

በታቦቱ ላይ የሚቀመጠው የማስተሰሪያ መስዋዕት የተሰራበት መክደኛ ወይም መሸፈኛ (ዘጸአት 25፡17 ተመልከት)

• በምስክሩ ታቦት ላይ አድርግ

የቃል ኪዳን ታቦት እንደማለት ነው። በድንጋይ ጽላት ላይ የተጻፉት ቃላት እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ለገባው ቃል ኪዳን ምስክር እንዲሆን ነው።

• ገበታውንም በሰሜን ወገን አድርገው

ይህ ገበታ የህሊዎተ እግዚአብሔር መገኛ ምሳሌ የሆነው ዳቦ ያለበት ነው። በሌላ አገላለጽ፦ ጠረጴዛውን/የዳቦ ማስቀመጫውን/ ከቅድስተ ቅዱሳኑ ክፍል ውጪ ከማደሪያ ድንኳን በስተ ሰሜን በኩል አኑር/አስቀምጥ/

Exodus 26:36

አጠቃላይ ምልከታ፦

የመገናኛውን ድንኳን እንዴት መገንባት እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል

• ከሰማያዊ ከሐምራዊም ከቀይም ግምጃ

ይህ አገላለጽ ሁለት ፍቺዎች አሉት፤ 1) በቀይ ቀለም የተቀባ ወይም የተነከረ ክር ወይም የሱፍ ጨርቅ 2) ሰማያዊ፥ ሐምራዊና ቀይ የሆነ ክር ወይም የሱፍ ጨርቅ።

• ከተፈተለ ከጥሩ በፍታ

በእጅ የተፈተለ ወይም የተሰራ የሱፍ ክርም ማግም ሊሆን ይችላል

• በጥልፍ አሠራር የተሠራ መጋረጃ

በጥልፍ ያጌጠ መጋረጃ ወይም በጥልፍ ዐዋቂ የተጠለፈ መጋረጃ


Chapter 27

1 ዐምስት ክንድ ወርዱም ዐምስት ክንድ የሆነ መሠዊያ ከግራር ዕንጨት ሥራ። መሠዊያው አራት ማእዘንና ሦስት ክንድ ከፍታ ይኑረው። 2 ማእዘኖች የበሬ ቀንድ ቅርጽ እንዲኖራቸው ታደርጋለህ። ቀንዶቹ ከመሠዊያው ጋር አንድ ወጥና በነሐስ የተለበጡ ይሆናሉ። 3 የመሠዊያውን ዕቃዎች፦ የዐምድ ማስወገጃ ምንቸቶችን፣ መጫሪያዎችን፣ ጎድጓዳ ሳሕኖችን፣ የሥጋ ሜንጦዎችንና የፍም መያዣዎችን ሁሉ ከነሐስ አብጃቸው። 4 ለመሠዊያው ከነሐስ እንደ መረብ የተሠራ ፍርግርግ አብጅለት። በፍርግርጉ አራት ማእዘኖች በያንዳንዳቸው ላይም የነሐስ ቀለበት አድርግ። 5 አጋማሽ ወገብ እስከ ታች እንዲደርስ ፍርግርጉን ከመሠዊያው እርከን ሥር አድርገው። 6 ለመሠዊያው መሎጊያዎችን ከግራር ዕንጨት አበጅተህ በነሐስ ለብጣቸው። 7 በቀለበቶቹ ውስጥ መግባትና መሠዊያውን ለመሸከም በሁለቱ ጎኖቹ ላይ መቀመጥ አለባቸው። 8 ባዶ እንዲሆን ከሳንቃዎች አብጀው። በተራራው ላይ ባየኸው መሠረት ልትሠራው ይገባል። 9 ድንኳን አደባባይ ሥራለት። በአደባባዩ ደቡብ ጎንም አንድ መቶ ክንድ እርዝመት ያላቸው የአማረ በፍታ መጋረጃዎች ይደረጉ። 10 መጋረጃዎቹ ከሃያ የነሐስ መቆሚያዎች ጋር ሃያ ምሰሶዎች ይኑሯቸው። ከምስሶዎቹ ጋር የተያያዙ የብር ኵላቦችና ዘንጎችም መኖር አለባቸው። 11 በሰሜን በኩልም እንደዚሁ አንድ መቶ ክንድ ርዝመት ያላቸው መጋረጃዎች ከሃያ ምሰሶዎች፣ ከሃያ የነሐስ መቆሚያዎችም ጋር ከምሰሶውቹ ጋር የተያያዙ የብር ኵላቦችና ዘንጎች ሊኖሩ ይገባል። 12 በአደባባዩ ምዕራብ ጎንም ዐምሳ ክንድ ርዝመት ያለው መጋረጃ ይደረግ። ዐሥር ምሰሶዎችና ዐሥር መቆሚያዎችም ይኑሩት። 13 በምሥራቅም በኩል አደባባዩ ዐምሳ ክንድ እርዝመት ይኑረው። 14 የመግቢያው አንድ ጎን መጋረጃዎች ዐሥራ ዐምስት ክንድ እርዝመት ሊኖራቸው ይገባል። ሦስት ምሰዎችም ከሦስት መቆሚያዎች ጋር ይኖሯቸዋል። 15 ሌላው ጎንም ዐሥራ ዐምስት ክንድ እርዝመት ያላቸው መጋረጃዎች ይኖሩታል። የራሳቸው ሦስት ምሰሶዎችና ሦስት መቆሚያዎች ይኖሯቸዋል። 16 መግቢያ መጋረጃ ሃያ ክንድ እርዝመት ያለው፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና አምሮ ከተፈተለ በፍታ ጠላፊ ጠልፎበት የተሠራ ይሁን። አራት ምሰሶዎች ከአራት መቆሚያዎች ጋር ሊኖሩት ይገባል። 17 የአደባዩ ምሰሶዎች ሁሉ የብር ዘንጎችና ኵላቦች፣ የነሐስ መቆሚያዎችም ይኑሯቸው። 18 የአደባባዩ እርዝመት አንድ መቶ ክንድ፣ ወርዱ ዐምሳ ክንድ፣ ቁመቱ ዐምስት ክንድ ይሁን፤ የበፍታ መጋረጃዎችና የነሐስ መቆሚያዎችም ይኑሩት። 19 በመገናኛው ድንኳን ውስጥ አገልግሎት የሚሰጥ ዕቃ ሁሉ፣ የድንኳኑ ካስማዎችም በሙሉ፣ አደባባዩም ከነሐስ መሠራት አለባቸው። 20 ሁልጊዜ እንዲበሩ ለመብራቶቹ የወይራ ጭማቂ ንጹሕ ዘይት እንዲያመጡ እስራኤላውያንን እዘዛቸው። 21 በመገናኛው ድንኳን ውስጥ፣ ከመጋረጃው ውጭ በምስክሩ ታቦት ፊት፣ አሮንና ልጆቹ መብራቶቹን ከማታ እስከ ንጋት ድረስ በእግዚአብሔር ፊት እንዲበሩ ያድርጉ። ይህም ለእስራኤል ትውልድ ሁሉ የዘለዓለም ሥርዐት ይሆናል።



Exodus 27:1

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• ርዝመቱ አምስት ክንድ፥ ወርዱም አምስት ክንድ

ዝርመቱ 2.3 ሜትር፥ የጉኑ ስፋት 2.3 ሜትር ያህል ነው

• ክንድ

አንድ ክንድ ወደ 46 ሴንት ሜትር ያህል ነው

• በአራቱም ማዕዘን ቀንዶችን ታደርጋለህ

በመሰዊያው አራቱም ማእዘን ጫፍ ላይ ቀንድ መሳይ ጒጦች /ነገር/ አውጣ

• ቀንዶቹም ከእርሱ ጋር በአንድ የተሠሩ ይሁኑ

ቀንዶቹም ከመሠዊያው ጋር አብሮ የተሠሩ ይሁን

Exodus 27:3

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• አመድ የሚሆንባቸውን ምንቸቶች

ለዐመድ ማጠራቀሚያነት የሚያገለግሉ ድስቶች /ድስት መሳይ ነገሮች/

• መጫሪያዎች

የእሳት መጫሪያዎች ወይም የእሳት መለኮሻዎች

• ዕቃውንም ሁሉ

በመሰዊያው ላይ ለመጠቀም የሚያገለግሉ ማንኛውንም ቁሳቁስ

• እንደ መረብ ሆኖ የተሠራ የናስ መከታ አድርግለት

እንደ መረብ ሆኖ የተሠራ የነሐስ መከላከያ አብጅለት/ሥራለት/

• የናስ መከታ

እንጨት በእሳት ሲቃጠል ለመያዝ የሚያገለግል ከነሐስ ብረት የተሰራ መያዣ

Exodus 27:5

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• መከታውም እስከ መሠዊያው እኵሌታ ይደርስ ዘንድ መሰዊያው በሚዞረው በእርከኑ ታች አድርገው

መከላከያው እስከ መሠዊያው እኩሌታ/ግማሽ/ ድረስ እንዲዘልቅ ከመሠዊያው ክፈፍ/ጫፍ በታች አድርገው/አስቀምጠው

• የናስ መከታ

እንጨት በእሳት ሲቃጠል ለመያዝ የሚያገለግል ከነሐስ ብረት የተሰራ መያዣ (ዘጸአት 27፡4 ተመልከት)

• መሎጊያዎች

መሠዊያውን ለመሸከም የሚያገለግሉ አግዳሚ እንጨቶች/ብረቶች/

Exodus 27:7

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• መሎጊያዎቹ በቀለበቶች ውስጥ ይግቡ፣ መሠዊያውን ስትሸከሙ መሎጊያዎቹ በሁለቱ ወገኖች ይሁኑ

በሌላ አገላለጽ፦ መሠዊያውን ለመሸከም አግዳሚ እንጨቶችን/ብረቶችን/ ከመሠዊያው በእያንዳንዱ ጐን ባሉት ቀለበቶች ውስጥ አግባ።

• ከሳንቆች ሠርተህ ባዶ አድርገው

ሳንቃ ከእንጨት ወይም ከብረት የተሰራ ጠፍጣፋ ነገር ነው። አማራጭ ትርጉም፦ መሠዊያው ውስጡ ባዶ ሆኖ ከሳንቃዎች መስራት አለብህ

• በተራራው ላይ ባሳየሁህ ዕቅድ መሠረት

ይህ ሀረግ ወይም ዓረፍተ ነገር በቀድሞ አማርኛ ትርጉም (በ1954/62) ላይ የተዘለለ/የተተወ ሀሳብ ነው። በዕብራይስጡና በሌሎች አማርኛና እንግሊዘኛ ትርጉሞች ይገኛል።

Exodus 27:9

• የማደሪያውን አደባባይ . . . የጥሩ በፍታ መጋረጆች ይሁኑለት

ለድንኳኑ አደባባይ ክልል የሚሆን ከቀጭን የሐር ክር (የጨርቅ ዓይነት) መጋረጃዎችን ሥራ

• የጥሩ በፍታ መጋረጆች

ቀጭን የሐር ክር ወይም ጨርቅ

• ርዝመት መቶ ክንድ ይሁን

ይህ ወደ 46 ሜትር የምያህል ርዝመት ያለው ነው።

• ለምሶሶቹ ኩላቦችና ዘንጎች የብር ይሁኑ

በምሶሶዎች ላይ ከብር ዘንጎችንና/ቋሚዎችንና/ መስቀያዎችን አድርግላቸው/ሥራላቸው/

Exodus 27:11

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• እንዲሁም . . . ከናስ የተሠሩ

ቁጥር 10 ለመተርጎም ቁጥር 9-10 ያለውን እንዴት እንደተረጎምክ ማየቱ የተሻለ ነው። ምክንያቱም ብዙ ተመሳሳይ ነገሮች ተጠቅሰዋል።

• የብር ኩላቦችና ዘንጎች ይሁኑ

ከብር የተሰሩ መስቀያዎችና ቋሚዎች አድርግ ወይም ከብር መስቀያዎችንና ቋሚዎችን ሥራ

• አምሳ ክንድ ርዝመት ያላቸው መጋረጆች

ሃያ ሶስት (23) ሜትር የሆነ መጋረጃዎችን ሥራ

• አሥር ምሰሶች

አስር ምሶሶዎችን ሥራ

• የአደባባዩ ስፋት አምሳ ክንድ

የአደባባዩ ስፋት 23 ሜትር አድርግ

Exodus 27:14

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• ሰማያዊ፥ ሐምራዊና ቀይ ግምጃ

አማራጭ ትርጉሞች፦ 1) በሰማያዊ፥ ሀምራዊና ቀይ ቀለም የተቀቡ ልብሶች/የሱፍ ጨርቆች/ ወይም 2) ላይነኖችን ለመቀባት የሚረዱ ሰማያዊ፥ ሐምራዊና ሰማያዊ ቀለም

• ለአደባባዩም ደጅ . . . ሃያ ክንድ መጋረጃ ይሆናል

ለአደባባዩ በር ወይም መግቢያ 9 ሜትር የሆነ መጋረጃ ሥራ

• ከጥሩ በፍታም በጥልፍ አሠራር የተሠራ ሀያ ክንድ መጋረጃ

ከጥሩ የሐር ክር የተሠራና የተፈተለ በጥልፍ ያጌጠ መጋረጃ

• በጥልፍ አሠራር የተሠራ

በጥልፍ ያጌጠና ያማረ መጋረጃ

Exodus 27:17

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• የአደባባዩ ርዝመት መቶ ክንድ ስፋቱም አምሳ ክንድ ይሁን

የድንኳኑ አደባባይ ርዝመቱ አርባ ስድስት ሜትር የጐኑ ስፋት ሃያ ሶስት ሜትር ሆኖ ይሰራ

• መጋረጃውም ከጥሩ በፍታ

መጋረጃው ከጥሩ /ከቀጭን/ የሐር ጨርቅ/ክር/ የተሰራ ይሁን ወይም መጋረጃውን ከጥሩ/ከቀጭን/ የሐር ጨርቅ/ክር/ ሥራ

• ለማገልገል ሁሉ የማደሪያው ዕቃ ሁሉ፥ ካስማዎቹም ሁሉ የአደባባዩም ካስማዎች ሁሉ፥ የናስ ይሁኑ

በድንኳኑ ውስጥ የሚገኙት ለማናቸውም አገልግሎት የሚውሉ የመገልገያ ዕቃዎችን ሁሉ፥ የድንኳኑንና የአደባባዩ ካስማዎችን ሁሉ ከነሐስ ብረት ሥራቸው።

• ካስማዎች

ከብረት ወይም ከእንጨት የተሰሩ በአንድ በኩል ሹል የሆኑ ድንኳን ለመወጠር የሚያገለግሉ ናቸው

Exodus 27:20

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• መገናኛው ድንኳን

በሌላ ስሙ የማደሪያ ድንኳን ተብሎ ይታወቃል

• የምስክር ታቦት

የቃል ኪዳን ታቦት ሲሆን በድንጋይ ጽላት ላይ የተጻፉት ቃላት እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ለገባው ቃል ኪዳን ምስክር እንዲሆን ነው።

• በእስራኤል ልጆች ዘንድ ለልጅ ልጃቸው የዘላለም ሥርዓት ይሁን

ይህ በእስራኤል ሕዝብና ወደፊት በሚነሣው ወይም በሚመጣው ትውልድ ዘንድ ቋሚ/የፀና/ ሥርዓት ሆኖ ይኑር/ይቀጥል/


Chapter 28

1 ሆነው እንዲያገለግሉኝ ወንድምህን ዘሮንንና ልጆቹን ናዳብን፣ አብድዩን፣ አልዓዛርንና ኢታምርን ከእስራኤል መካከል ወደ አንተ ጥራ። 2 ለወንድምህ ለአሮን ለእኔ የተቀደሱ ልብሶችን አዘጋጅ። እነዚህ ልብሶች ለአሮን ክብርና ማዕርግ የሚሆኑ ናቸው። 3 ካህኔ ሆኖ እንዲያገለግለኝ የአሮንን ልብሶች የሚሠሩለትን፣ በልባቸው ጥበበኛ የሆኑትን፣ የጥበብን መንፈስም የሞላሁባቸውን ሰዎች ሁሉ አነጋግር። 4 የሚሠሯቸው ልብሶችም የደረት ኪስ፣ ኤፉድ፣ ቀሚስ፣ ጥልፍ የተጠለፈበት ሸሚዝ፣ መጠምጠሚያና መታጠቂያ ናቸው። ለእኔ የተቀደሱትን እነዚህን ልብሶች መሥራት አለባቸው። ልብሶቹ ካህናት ሆነው እንዲያግለግሉኝ ለወንድምህ ለአሮንና ለልጆቹ ይሆናሉ። 5 ወርቅ፣ ሰማያዊ፣ ሐምራዊ፣ ቀይ ማግና የአማረ በፍታ ይጠቀሙ። 6 ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግን ኣአምሮ ከተፈተለ በፍታ ይሥሩት። ሥራው የብልኀተኛ ሙያተኝ ሥራ ሊሆን ይገባል። 7 ኤፉዱ ከሁለቱ ጠርዞቹ ጋር የሚያያዙ ሁለት የትከሻ ንጣዮች ይኑሩት። 8 በብልኀት የተጠለፈው የወገብ መታጠቂያም እንደ ኤፉድ መሆን አለበት፦ ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና አምሮ ከተፈተለ በፍታ ወጥ ሆኖ የተሠራ ይሁን። 9 ሁለት የመረግድ ድንጋዮችን ወስደህ የዐሥራ ሁለቱን የእስራኤል ልጆች ስሞች ቅረጽባቸው። 10 ስድስቱ ስሞቻቸው በአንድ ድንጋይ፣ ስድስቱ ሌሎች ደግሞ በሌላው ድንጋይ ላይ እንደየልጁ ልደት ቀደም ተከተል ይቀረጹ። 11 ሠራተኛ ማኅተም እንደሚቀርጽ የእስራኤልን ዐሥራ ሁለት ልጆች ስሞች በሁለቱ ድንጋዮች ላይ ቅረጽ። ድንጋዮቹንም በወርቅ ክፈፋቸው። 12 ሁለቱን ድንጋዮች የእስራኤልን ልጆች አምላክ የሚያስታውሱ ድንጋዮች እንዲሆኑ በኤፉዱ የትከሻ ንጣዮች ላይ አስቀምጥ። መታሰቢያ እንዲሆኑ አሮን ስሞቻቸውን በሁለቱ ትከሻዎቹ ላይ በእግዚአብሔር ፊት ይሸከማል። 13 ፈርጦችንና 14 እንደ ገመድ የተጎነጎኑ የንጹሕ ወርቅ ድሪዎችን አበጅተህ ከፈርጦቹ ጋር አያይዛቸው። 15 ብልኅ ሠራተኛ እንደሚሠራው፣ ኤፉዱ በተሠራበት መንገድ ፍርድ የሚሰጥበትን የደረት ኪስ አብጅ። ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና አምሮ ከተፈተለ በፍታ ሥራው። 16 አራት ማእዘን ያለ ውይሁን። የደረት ኪሱን ዐጥፈህ ድርብ አድርገው። አንድ ስንዝር እርዝመት፣ አንድ ስንዝር ስፋትም ይኑረው። 17 ዕንቆችን በአራት ረድፍ አስቀምጥ። የመጀመሪያው ረድፍ ሰርድዮን፣ ቶነዝዮንና አብረቅራቂ ዕንቊ ሊኖሩት ይገባል። 18 ሁለተኛው ረድፍ በሉር፣ ሰንፔርና አልማዝ ይኑሩት። 19 ሦስተኛው ረድፍ ያክንት፣ ኬልቄዶንና አማቴስጢኖስ ይገኙበታል። 20 አራተኛው ረድፍ ቢረሌ፣ መረግድና ኢያስጲድ ይኑሩት። በወርቅ ፈርጥ ክፈፍ ሊደረግላቸው ይገባል። 21 ድንጋዮቹ በዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ልጆች ስሞች ቅደም ተከተል መሠረት መቀመጥ፣ ከእስራኤል ነገዶች አንዱን በመወከልም በቀለበት ማተሚያ እንደሚቀረጽ እያንዳንዱ ስም የተቀረጸባቸው መሆን አለባቸው። 22 ኪሱ ከንጹሕ ወርቅ እንደ ገመድ የተጎነጎኑ ድሪዎችን አብጅለት። 23 ሁለት የወርቅ ቀለበቶችን ሥራና ከደረት ኪሱ ሁለት ጎኖች ጋር አያይዛቸው። 24 የወርቅ ድሪዎች ከደረት ኪሱ ሁለት ማእዘኖች ጋር አያይዛቸው። 25 ጕንጕን ድሪዎች ሌሎች ጎኖች ከሁለቱ የወርቅ ፈርጦች ጋር አገናኛቸው። ከኤፉፉ የትከሻ ንጣዮች ጋርም በፊቱ በኩል አያይዛቸው። 26 የወርቅ ቀለበቶችን ሥራና ከውስጠኛው የኤፉዱ ጎን ቀጥሎ ባለው ጠርዝ ላይ፣ በደረት ኪሱ ሌሎች ሁለት ጎኖች ላይ አድርጋቸው። 27 ሁለት ተጨማሪ የወርቅ ቀለበቶችን አብጅና በብልኀት ከተጠለፈው ከሴፉዱ መታጠቂያ በላይ፣ መጋጠሚያው አጠገብ ከኤፉዱ ፊት ሁለት የትከሻ ንጣዮች ግርጌ ጋር አያይዛቸው። 28 ከኤፉዱ መታጠቂያ በላይ መያያዝ እንዲችሉ፣ የደረት ኪሱን ቀለበቶቹ ከኤፉዱ ቀለበቶች ጋር በሰማያዊ ገመድ ማሰር አለባቸው። ይህም የሚሆነው የደረት ኪሱ ከኤፉዱ ጋር ሳይያያዝ እንዳይቀር ነው። 29 አሮን ወደ መቅደሱ በገባ ጊዜ፣ የዐሥራ ሁለቱን የእስራኤል ልጆች ስሞች በደረት ኪሱ ላይ ለፍርድ በልቡ ላይ ይሸከም። ይህም በእግዚአብሔር ፊት የዘለዓለም መታሰቢያ ሆኖ ያገለግላል። 30 በፍርድ መስጫው የደረት ኪስ ውስጥ ኡሪምንና ቱሚምን አስቀምጥ። አሮን ወደ እግዚአብሔር ፊት ሲቀርብ፣ ኡሪምና ቱሚም በደረቱ ላይ መኖር አለባቸው፤ አሮንም ለእስራኤል ፍርድ መስጫውን በእግዚአብሔር ፊት ሲቀርብ ሁልጊዜ መሸከም ይኖርበታል። 31 ቀሚስ ሙሉ በሙሉ ሰማያዊ ይሁን። 32 ለራስ ማስገቢያ ክፍተት ይኑረው፤ ክፍተቱም እንዳይቀደድ ዙሪያውን የተዘመዘመ ጠርዝ ይኑረው። ይህ ሥራ የሸማኔ ሥራ መሆን አለበት። 33 የግርጌ ጠርዝ ላይ የሰማያዊ፣ የሐምራዊና የቀይ ማግ ሮማኖችን በዙሪያው አድርግ። በመካከላቸውም ዙሪያውን የወርቅ ሻኵራዎችን አብጅ። 34 የወርቅ ሻኵራዎቹና ሮማኖቹ በቀሚሱ ጠርዝ ዙሪያ እየተፈራረቁ መቀመጥ አለባቸው። 35 ወደ መቅደሱ ሲገባና በእግዚአብሔር ፊት ሲሆን፣ ከመቅደስ ሲወጣም፣ ድምፁ እንዲሰማ ቀሚሱን አሮን ሲያገለግል ይልበሰው። ይህም የሚደረገው አሮን እንዳይሞት ነው። 36 ከንጹሕ ወርቅ ሳሕን አብጅና በቀለበት ላይ ማኅተም እንደሚቀረጽ፣ “ቅዱስ ለእግዚአብሔር” ብለህ በላዩ ቅርጽበት። 37 ሳሕን ከመጠምጠሚያው ፊት ጋር በሰማያዊ ገመድ አያይዘው። 38 ሁልጊዜም በአሮን ግንባር ላይ ይሁን፤ አሮን እስራኤላውያን ለእግዚአብሔር ለይተው ከሚያቀርቧቸው የተቀደሱ ስጦታዎች ጋር የሚያያዝ ማንኛውንም በደል ይሸከማል። እግዚአብሔር ስጦታዎቻቸውን እንዲቀበል፣ መጠምጠሚያ ሁልጊዜ በአሮን ግንባር ላይ መሆን አለበት። 39 ሸሚዙንም፣ መጠምጠሚያውንም ከአማረ በፍታ ትሠራለህ። መታጠቂያውም በጥልፍ ጠላፊ እንዲሠራ ታደርጋለህ። 40 ለአሮን ልጆችም ሸሚዞቹን፣ መታጠቂያዎችንና የራስ ማሰሪያዎችን ለክብራቸውና ለማዕረጋቸው ታደርጋለህ። 41 ለወንድምህ ለአሮንና ለልጆቹ አልብሳቸው። ቅባቸው፣ ሹማቸውም፤ ካህናት ሆነው እንዲያገለግሉኝም ለእኔ ቀድሳቸው። 42 እስከ ጭን የውስጥ ሰውነታቸውን የሚሸፍን የውስጥ ልብሶችን ከበፍታ ሥራ። 43 ልጆቹ ውደ መገናኛው ድንኳን ሲገቡ፣ ወይም መቅደሱ ውስጥ ለማገልገል ወደ መሠዊያው ሲቀርቡ እነዚህን የውስጥ ልብሶች መልበስ አልባቸው። በደል እንዳይገኝባቸውና እንዳይሞቱ ይህን ማድረግ ይገባቸዋል። ይህ ለአሮንና ከእርሱም በኋላ ለሚመጡት ዘሮቹ የዘለዓለም ሥርዓት ይሆናል።



Exodus 28:1

• ወደ አንተ አቅርብ

“ወደ አንተ” የተባለው ሙሴ ነው። በሌላ አገላለጽ፦ ወደ አንተ ጥራቸው

• ናዳብን አብዩድንም አልዓዛርንም ኢታምርንም

የወንዶች ስም ዝርዝር ነው (ስሞችን የመተርጎም ዘዴ ተመልከት)

• ልብስ እንዲሠሩለት

ይህ በወል ስም የተጠቀሰው “የእስራኤላውያንን” የሚመለከት ነው

• ቅዱስ ይሆን ዘንድ

ለእኔ የተለየ እንዲሆን

Exodus 28:4

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ዝንጕርጕር ሸሚዝም

ባጌጠ ጥልፍ የተሰራና በእፉዱ ላይ በውጭ በኩል የሚለበስ ልብስ ወይም ኮት። ነገር ግን እንደ ዛሬው የሸሚዝ ዓይነት ከጃኬት ወይም ከኮት ሥር የሚለበስ አይደለም

• መጠምጠሚያ

ረዘም ያለ ከልብስ/ከጨርቅ/ የተሰራ በራስ ላይ የሚጠመጠም ነው

• መታጠቂያ

ከልብስ/ከጨርቅ/ የተሰራ በወገብ ላይ ወይም በደረት ላይ የሚለበስ

Exodus 28:6

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ከተፈተለ ከጥሩ በፍታም

በቀጭኑ ከተፈተለ ከተጠመዘዘ ሐር ጨርቅ/ክር/ ወይም ከላይነን ጨርቅ ሥሩ

• ብልህ ሠራተኛ እንደሚሠራ (ዘጸአት 26፡36 ተመልከት)

የጥልፍ ዐዋቂዎች በጥልፍ አስጊጠው ይሥሩ

• ሁለቱ ወገን አንድ እንዲሆን

መተሳሰር ወይም መያያዝ እንዲችል ሆኖ

• የመረግድ ድንጋይ

ይህ የተመረጠ ወይም የከበረ ድንጋይ የሚባለው ድንጋይ ዘር ሲሆን የተለያየ ቀለም ያለው የድንጋይ ዓይነት ለምሳሌ ነጭ፥ ጥቁር፥ ቀይ ወይም ሰማያዊ ቀለም አለው።

Exodus 28:10

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• በቅርጽ ሠራተኛ ሥራ እንደ ማኅተም ቅርጽ

የቅርጽ ሠራተኛ ማኅተም እንደሚቀርጽ አደርገህ

• የቅርጽ ሠራተኛ

የቅርጽ ሠራተኛ በጠንካራ ነገር ላይ ለምሳሌ በድንጋይ፥ በብረት ወይም በእንጨት ላይ በመቅረጽ የሚሰራ ማለት ነው።

• በኤፉዱ ጫንቃዎች ላይ ታደርጋለህ

በኤፉዱ ትከሻ ላይ ካሉት ንጣዮች ጋር አያይዛቸው

Exodus 28:13

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• በኤፉዱ ጫንቃዎች ላይ ታደርጋለህ

በኤፉዱ ትከሻ ላይ ካሉት ንጣዮች ጋር አያይዛቸው (28፡11 ተመልከት)

• የወርቅም ፈርጦች ሁለትም ድሪዎች ሥራ

ሁለት የወርቅ ፈርጦች ሥራ

Exodus 28:15

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ብልህ ሠራተኛም እንደሚሠራ የፍርዱን የደረት ኪስ ሥራው

የፍርድ መስጫውን ወይም የእግዚአብሔር ፈቃድ መጠየቂያውን የደረት ኪስ ብልኅ ሠራተኛ እንደሚሠራው አድርገህ ሥርው

• ስንዝር

አንድ ስንዝር ወደ ሃያ ሁለት ሴንት ሜትር ያህል ነው።

Exodus 28:17

አጠቃላይ ዕይታ፦

ዕይታ፦ በዚህ ሥፍራ አስራ ሁለት የድንጋይ ዓይነቶች ተዘርዝረዋል። በዕብራይስጥ የትኛው ቃል የትኛውን የድንጋይ ዓይነት እንደሚገልጽ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን እርግጠኛ አይደሉም። አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጅዎች የተለያየ የድንጋይ ዓይነት ዝርዝር ያቀርባሉ።

• የከበረ ድንጋይ

በአማርኛ ቅጅዎች የከበሩ ድንጋዮች ወይም ዕንቁዎች ተብለው ይታወቃሉ።

• የመረግድ ድንጋይ

ይህ የተመረጠ ወይም የከበረ ድንጋይ የሚባለው ድንጋይ ዘር ሲሆን የተለያየ ቀለም ያለው የድንጋይ ዓይነት ለምሳሌ ነጭ፥ ጥቁር፥ ቀይ ወይም ሰማያዊ ቀለም አለው።

• ሰርድዮን፥ ቶጳዝዮን . . . ኢያስጵድ

እነዚህ የከበሩ ድንጋዮች ወይም ዕንቁዎች ናቸው

• ሰንፔር

የከበረ ድንጋይ ወይም ዕንቁ ሲሆን ቀለሙ ሰማያዊ ነው።

• በወርቅ ፈርጥ ይደረጋሉ

በወርቅ ፈርጥ ላይ ይቀመጣሉ

Exodus 28:21

አጠቃላይ ምልከታ፦

ምልከታ፦ እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የዕንቆቹም ድንጋዮች እንደ እስራኤል ልጆች ስሞች አሥራ ሁለት ይሆናሉ

ለእያንዳንዱ የእስራኤል ልጆች ስም ዐሥራ ሁለት ድንጋዮች ይሁኑ/ይሰሩ/

• በየስማቸውም ማተሚያ እንደሚቀረጽ ይቀረጹ

የዐሥራ ሁለቱ ነገዶች ስሞች እንደ ማኅተም የተቀረጸባቸው (ዘጸአት 28፡11 ተመልከት)

• የተጎነጎኑትን ድሪዎች እንደ ገመድ አድርገህ ከጥሩ ወርቅ ሥራቸው

እንደ ገመድ የተጐነጐነ ወይም እንደ ገመድ ሆኖ የተጌጠ የወርቅ ድሪ ከንጹሕ ወርቅ ሥራ (ዘጸአት 28፡14 ተመልከት)

Exodus 28:25

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የወርቅ ፈርጦች

እንደ ገመድ የተገመዱ የወርቅ ፈርጦች

• ሁለት የወርቅ ቀለበቶችም ሥራ፥ እነርሱንም በኤፉዱ ፊት ለፊት ባለው በደረቱ ኪስ በሁለቱ ጫፎች ላይ ታደርጋቸዋለህ

እነዚህ ሁለት የወርቅ ከበቶች ኤፉዱን በሁለት በኩል የሚያቅፉ ናቸው (ዘጸአት 28፡14)። አማራጭ ትርጉም፦ ሁለት የወርቅ ቀለበቶች ሠርተህ በውስጥ በኩል ከኤፉዱ ቀጥሎ ባለው የደረት ኪስ ከታችኛዎቹ ማእዘኖች ጋር እንዲያያዙ አድርገህ ሥራ።

Exodus 28:27

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• በብልሃት የተጠለፈ የኤፉዱ ቋድ

በብልኀት ከተጠለፈው ወይም በጥልፍ ያጌጠው የኤፉድ መታጠቂያ

• ከኤፉዱም እንዳይለይ፥ የደረቱን ኪስ ከቀለበቶቹ ወደ ኤፉዱ ቀለበቶች በሰማያዊ ፈትል ያስሩታል

ከኤፉዱ ጋር እንዳይላቀቅ፣ ከኤፉድ መታጠቂያ ጋር በማገናኘት በሰማያዊ ገመድ ከኤፉዱ ቀለበቶች ጋር መያያዝ አለበት

Exodus 28:29

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• በእግዚአብሔር ፊት ለዘላለም መታሰቢያ የእስራኤልን ልጆች ስሞች በፍርዱ በደረት ኪስ ውስጥ በልቡ ላይ ይሸከም

በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ለዘላለም መታሰቢያ ይሆን ዘንድ የእስራኤልን ልጆች ስሞች በፍርድ መስጫው ደረት ኪስ በልቡ ላይ ይሸከም (ዘጸአት 28፡17-21 ተመልከት)

• በልቡ ላይ ይሸከም

አሮን በልቡ ላይ ወይም በደረቱ ላይ ይሸከም

• በፍርዱ በደረት ኪስም ውስጥ ኡሪምንና ቱሚምን ታደርጋለህ፣

ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በሚገባበት ጊዜ በአሮን ልብ ላይ ይሆኑ ዘንድ ኡሪሙንና ቱሚሙን በደረት ኪሱ አድርግ

• ኡሪምና ቱሚም

እነዚህ ነገሮች ምን እንደሆኑ አይታወቅም ነገር ግን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ የሚረዱ ድንጋዮች ሳይሆኑ አይቀሩም።

Exodus 28:31

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የኤፉዱን ቀሚስ

በኤፉዱ መደረቢያ ቀሚስ ወይም ረጅም ልብስ

Exodus 28:33

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ሮማን

የፍራፍሬ ዛፍ ሲሆን ክብ የሆነ የፍሬው ውጫዊ ክፍሉ ቀይ ነው።

• ወርቅ ሻኵራ ሮማን

ሮማን የሚመስለው የወርቅ መርገፍ ወይም ጸናጽል

• በማገልገል ጊዜም በአሮን ላይ ይሆናል

አሮን በክህነት በሚያገለግልበት ጊዜ ይህን ቀሚስ መልበስ አለበት

• በእግዚአብሔር ፊት ሲገባና ሲወጣ ድምፁ ይሰማል

በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወደ መቅደሱ ሲገባና ከመቅደሱ ሲወጣ የጸናጸሎች ድምፅ ይሰማል

• እርሱም እንዳይሞት

ይህ የሚያሳየን አሮን በትክክል እግዚአብሔርን ካልታዘዘ እንደሚሞት ነው። በሌላ አገላለጽ፦ ምክንያቱም አሮን እንዳይሞት

Exodus 28:36

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• በእርሱም እንደ ማኅተም ቅርጽ አድርገህ

በማኅተም ላይ እንደሚቀረጽ ቅረጸው (ዘጸአት 28፡11 ተመልከት)

• መጠምጠሚያ

ረዘም ያለ ከልብስ/አጨርቅ/ የተሰራ በራስ ላይ የሚጠመጠም

• በአሮንም ግምባር ላይ ይሆናል

አሮንም በግንባሩ ላይ ያድርገው ወይም ይልበሰው

Exodus 28:39

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• መጠምጠሚያ

ረዘም ያለ ከልብስ/አጨርቅ/ የተሰራ በራስ ላይ የሚጠመጠም

• መታጠቂያ

ከልብስ/ከጨርቅ/ የተሰራ በወገብ ላይ ወይም በደረት ላይ የሚለበስ (ዘጸአት 28፡4)

• በጥልፍ አሠራር

በጥልፍ ጥበብ ወይም በጥልፍ ጠላፊ ያጌጠ ይሁን

Exodus 28:40

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• መታጠቂያ

ከልብስ/ከጨርቅ/ የተሰራ በወገብ ላይ ወይም በደረት ላይ የሚለበስ (ዘጸአት 28፡4 ተመልከት)

• ቆቦች

ከጨርቅ የተሰሩ ጠበብ ያሉ የራስ ማሰሪያዎችን

• አሮንን ከእርሱም ጋር ልጆቹን ታለብሳቸዋለህ

በሌላ አገላለጽ፦ እነዚህን ልብሶች አሮንና ወንድ ልጆቹን ታለብሳቸዋለህ

Exodus 28:42

አጠቃላይ ምልከታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• የበፍታ ሱሪ ታደርግላቸዋለህ፣ ከወገባቸውም እስከ ጭናቸው ይደርሳል

ከጥሩ በፍታ (ሐር ጨርቅ/ክር/ የተሰራ ከወገባቸው እስከ ጭናቸው የሚደርስ ቊምጣ ሱሪ ወይም የውስጥ ሱሪ ሥራላቸው

• መገናኛው ድንኳን

ማደሪያው ድንኳን ሌላ ስሙ ነው (27፡1 ተመልከት)

• ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ለዘላለም ሥርዓት ይሆናል

ይህ እንግዲህ ለአሮንና ለትውልዱ ሁሉ ጸንቶ የሚኖር (የማይለወጥ) ሥርዓት ይሆናል


Chapter 29

1 ሆነው እንዲያገለግሉኝ እነርሱን ለእኔ ለመቀደስ አሁን የምታደርገው ይህ ነው። ነውር የሌለባቸውን አንድ ወይፈንና ሁለት አውራ በጎች፣ 2 የሌለበትን እንጀራና ዘይት የተቀላቀለበትን እንጎቻ ውሰድ፤ ዘይት የተቀባ ስስ ቂጣም አድርግ። 3 በአንድ ሌማት አድርጋቸውና ከወይፈኑና ከአውራ በጎቹ ጋር አቅርባቸው። 4 አሮንንና ልጆቹንም ወደ መገናኛ ድንኳኑ መግቢያ አቅርባቸው። በውሀም እጠባቸው። 5 ውሰድና፦ ሸሚዙን፣ የኤፉዱን ቀሚስ፣ ኤፉዱን፣ የደረት ኪሱን፣ በብልኀት የተጠለፈውን የኤፉዱን መታጠቂያ በወገቡ ዙሪያ በማስታጠቅ አሮን አልብሰው። 6 ቅዱሱን አክሊል በላዩ አስቀምጠህ መጠምጠሚያውን በአሮን ራስ አድርግ። 7 ዘይቱንም ወስደህ በራሱ ላይ በማፍሰስ ቅባው። 8 አምጥተህ ሸሚዞችን አልብሳቸው። 9 መታጠቂያዎችን ለአሮንና ለልጆቹ ታስታጥቃቸዋለህ፤ የራስ ማሰሪያዎችንም ታደርግላቸዋለህ። የክህነቱ ሥራ በዘለዓለማዊ ሕግ የእነርሱ ይሆናል። እኔን እንዲያገለግሉኝ አሮንና ልጆቹን ትክናቸዋለህ። 10 በመገናኛው ድንኳን ፊት አቅርብ፤ አሮንና ልጆቹም በወይፈኑ ራስ ላይ እጆቻቸውን ይጫኑ። 11 በእኔ በእግዚአብሔር ፊት በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ዕረደው። 12 ከወይፈኑ ደም ጥቂት በጣትህ ወስደህ በመሠዊያው ቀንዶች ላይ ታደርጋለህ፤ 13 የሆድ እቃዎችን የሚሸፍነውን ስብ ሁሉ ጉበቱን የሚሸፍነውንና ሁለቱን ኩላሊቶች በላያቸው ካለው ስብ ጋር ወስደህ ሁሉንም በመሰዊያው ላይ ታቃጥላቸዋለህ። 14 ነገር ግን የወይፈኑን ሥጋ ግን ቁርበቱንና ፈርሱን ጭምር ከሰፈር ውጭ አውጥተህ ታቃጥላለህ። ያ የኀጢአት መሥዋዕት ይሆናል። 15 የአውራ በግም ውሰድና አሮንና ልጆቹ እጆቻቸውን ይጫኑበት። 16 በጉን ዕረደው፤ ደሙንም ወስደህ በመሠዊያው ላይ ዙሪያውን እርጨው። 17 በጉን ለሁለት ክፈልና የሆድ ዕቃውንና እግሮቹን እጠብ፤ የሆድ ዕቃውንም ከተቆራተጡ ብልቶችና ከራሱ ጋር 18 ላይ አስቀምጥ። ከዚያም እውራ በጉን ሙሉ በሙሉ አቃጥለው። ለእኔ ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት ይሆናል። ይህም ለእኔ ጣፋጭ መዐዛ ያለው፣ በእሳት የቀረበልኝ መሥዋዕት ይሆናል። 19 ሌላውንም አውራ በግ ወስደህ አሮንና ልጆቹ እጆቻቸውን በራሱ ላይ ይጫኑበት። 20 በኋላ አውራ በጉን ዕረደው፤ ከደሙም ጥቂት ውሰድና በአሮን ቀኝ ጆሮ ጫፍና በልጆቹ ቀኝ ጆሮዎች ጫፍ ላይ፣ በቀኝ እጆቻቸውና በቀኝ እግሮቻቸው አውራ ጣቶች ላይ አድርግ። ደሙን በመሠዊያው ላይ ዙሪያውን እርጨው። 21 ካለው ደም፣ ከመቅቢያው ዘይትም ጥቂት ውሰድና በአሮንና በልብሶቹ፣ በልጆቹና በልብሶቻቸውም ላይ እርጨው። አሮንና ልብሶቹ፣ ልጆቹና ልብሶቻቸው ከእርሱ ጋር ይቀደሱልኛል። 22 በጉን ሥብ፣ ላቱን፣ ሆድ ዕቃውን የሚሸፍነውን ሥብ፣ የጉበቱን መሸፈኛ፣ ሁለቱን ኵላሊቶችና በላያቸው የሚገኘውን ሥብ፣ የቀኙን ወርችም ውሰድ፤ ይህ አውራ በግ ካህኑ ለእኔ የሚቀደስበት ነውና። 23 እንጀራ፣ አንድ በዘይት የተጋገረ እንጎቻና አንድ ስስ ቂጣ በእኔ በእግዚአብሔር ፊት ከሚሆነው ያለ እርሾ ከተጋገረው ኅብስት ሌማት ትወስዳለህ። 24 እነዚህን በአሮን እጆችና በልጆቹ እጆች ታስቀምጣለህ። እነርሱ በእኔ በእግዚአብሔር ፊት ይወዝውዟቸው፤ መሥዋዕት አድርገውም ለእኔ ያቅርቧቸው። 25 ከእጆቻቸው ወስደህ ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር በመሠዊያው ላይ አቃጥለው። ለእኔ ጣፋጭ መዐዛ ያለው፣ በእሳት የቀረበልኝ መሥዋዕት ይሆናል። 26 የአሮንን የክህነት አውራ በግ ፍርምባ ወስደህ ወዝውዘውና መሥዋዕት አድርገህ ለእኔ ለእግዚአብሔር አቅርበው። ይህም አንተ የምትበላው የአንተ ድርሻ ይሆናል። 27 የመሥዋዕቱን ፍርምባና የቀረበውን የመሥዋዕቱን ወርች ለእኔ ቀድስልኝ፤ ሁለቱም አሮንና ልጆቹ ለእኔ ካህናት መሆናቸውን ለማረጋገጥ ከአውራ በጉ የሚገኙ ናቸው። 28 የሚሰጧቸው እነዚህ የሥጋ ክፍሎች ምንጊዜም የአሮንና የልጆቹ ናቸው። በኅብረቱ መሥዋዕቶች ሥርዐት፣ ከእስራኤላውያን ለካህናቱ፣ ለእኔ ለእግዚአብሔር የሚቀርቡ መሥዋዕቶች ይሆናሉ። 29 የአሮን የተቀደሱ ልብሶች ከእርሱ በኋላ ለልጆቹም ይሆናሉ። በልብሶቹ የአሮን ልጆች ለእኔ መቀባትና መካን አለባቸው። 30 በቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ እኔን ለማገልገል ወደ መገናኛው ድንኳን የሚገባ፣ አሮንን ከልጆቹ መካከል የሚተካ እነዚያን ልብሶች ሰባት ቀን ይልበስ። 31 የክህነቱን አውራ በግ ውሰድና ሥጋውን በተቀደሰ ስፍራ ቀቅለው። 32 ልጆቹ የአውራ በጉን ሥጋና በመገናኛው ድንኳን መግቢያ በር ባለው ሌማት የተቀመጠውን ኅብስት ይብሉት። 33 ለማስተስረይና ለእኔ እንዲቀደሱ የቀረቡትን ሥጋውንና ኅብስቱን መብላት አለባቸው። ሌላ ሰው መብላት አይችልም፤ ምክንያቱም ምግቡን ለእኔ የተቀደሰ አድርገው ሊይዙት ይገባል። 34 መሥዋዕቱ ሥጋ፣ ወይም ከኅብስቱ እስከሚቀጥለው ጠዋት ድረስ አንዳች የሚተርፍ ከሆነ፣ አቃጥለው። ለእኔ የተቀደሰ ስለ ሆነ መበላት የለበትም። 35 በዚህ መንገድ እንድታደርገው ያዘዝሁህን ሁሉ በመከተል ለአሮንና ለልጆቹ ትፈጽምላቸዋለህ። እነርሱን ሰባት ፍቀን ቀድስልኝ። 36 ለስርየት የሚሆን የኀጢአት መሥዋዕት በየቀኑ አንድ ወይፈን አቅርብ። ማስተሰረያውን በማድረግም መሠዊያውን አንጻ፤ ለእኔ ለመቀደስም ቅባው። 37 ሰባት ቀን ማስተሰረያ አድርግለትና ለእግዚአብሔር ቀድሰው። ከዚያ በኋላ መሠዊያው ሙሉ በሙሉ የተቀደሰ ይሆናል፤ መሠዊያውን የሚነካውም ሁሉ ይቀደሳል። 38 የአንድ ዓመት ጠቦቶችን ዘወትር በየቀኑ በመሠዊያው ላይ አቅርብ። 39 ጠቦት ማለዳ፣ ሌላውን ደግሞ ምሽት ላይ ታቀርበዋህ። 40 ከመጀመሪያው ጠቦታ ጋር የኢፍ አንድ ዐሥረኛን ያማረ ዱቄት ተወቅጦ ከተጠለለ ሩብ ኢፍ ዘይት ጋር በመለወስ፣ ሩብ ወይንንም የመጠጥ ቍርባን በማድረግ አቅርብ። 41 ሁለተኛውን ጠቦት በምሽት ሠዋው። በማለዳ እንደ ተሠዋው ጠቦት ተመሳሳይ የእህልና የመጠት ቍርባን ማቅረብ አለብህ። እነዚህ መሥዋዕቶች ለእኔ ጣፋጭ መዐዛ ያላቸው በእሳት የቀረቡልኝ መሥዋዕቶች ናቸው። 42 ትውልዶች ሁሉ ዘወትር የሚቀርቡ የሚቃጠሉ መሥዋዕቶች ናቸው። ላናግራችሁ ከእናንተ ጋር በምገናኝበት በመገናኛው ድንኳን መግቢያ በር በእኔ በእግዚአብሔር ፊት መሥዋዕቶቹን አቅርቧቸው። 43 ከእስራኤላውያን ጋር የምገናኝበት ቦታ ያ ነው፤ ድንኳኑ በክብሬ ይቀደስልኛል። 44 የመገናኛውን ድንኳንና መሠዊያውን የእኔ ብቻ እንዲሆኑ እቀድሳቸዋለሁ። ካህናት ሆነው እንዲያገለግሉኝ አሮንንና ልጆቹን እለያቸዋለሁ። 45 በእስራኤላውያን መካከል እኖራለሁ፤ አምላካችውም እሆናለሁ። 46 በመካከላቸው እንድኖር፣ ከግብፅ ምድር ያወጣኋቸው እኔ እግዚአብሔር አምላካችው እንደ ሆንሁ ያውቃሉ።



Exodus 29:1

• የምታደርግባቸው ነገር ይህ ነው

እግዚአብሔር የካህናት ልብስ ዝግጅትና አሰራር ላይ የሰጠውን መመሪያ ጨርሶ ወደ ካህናትን ወደ መቀደስ ሥርዓት ሲሻገር እናያለን።

• የምታደርግባቸው ነገር ይህ ነው

ይህን የሚሰራው ሙሴ እንደ ሆነ ማመልከቱ ነው።

• ትቀድሳቸው ዘንድ

አሮንና ልጆቹ ካህናት ሆነው በፊቴ ወይም እኔን እንዲያገለግሉኝ የምትለያቸው

• እንዲያገለግሉኝ

በአንደኛ መደብ የተገለጸው እግዚአብሔር /ያህዌ/ ነው። በሌላ አገላለጽ፦ “እኔን እንዲያገለግሉ”

• አንድ ወይፈን

ቀንበር ያልተቀመጠበት ወጣት በሬ ማለት ነው

• ቂጣ እንጀራ፥ በዘይትም የተለወሰ የቂጣ እንጎቻ

እርሾ ያልነካው በወይራ ዘይት የታሸ ወይም ወይራ ዘይት የመጨመረበት ቂጣ

• በዘይትም የተቀባ ስስ ቂጣ ከመልካም ስንዴ

ምርጥ የሆነ የስንዴ ዱቄት ወስደህ ስስ/ቀጭን/ ቂጣ ጋግረህ ዘይት ቀባው

Exodus 29:3

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• በአንድ ሌማትም ታደርጋቸዋለህ

“ሌማት” የተባለው የዳቦ/የቂጣ/የእንጀራ/ ወይም ሌላ ምግብ ማስቀመጫ የሚያመለክት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ሁሉንም በመሶብ ወይም በቅርጫት መሳይ ነገር ታስቀምጣቸዋለህ/ ታኖራቸዋለህ/

• ከወይፈኑና ከሁለቱ አውራ በጎች ጋር በሌማቱ ታቀርባቸዋለህ

በዚህ ክፍል “ታቀርባቸዋለህ” የሚለው መስዋዕት ማቅረብን የሚመለከት ነው። በሌላ አገላለጽ፦ አንድ ኰርማ/ወይፈን/ እና ሁለቱን አውራ በጎች በምትሠዋበት ጊዜ ለእኔ መባ/መስዋዕት/ አድርገህ አቅርብልኝ/ሰዋልኝ/

• መገናኛው ድንኳን

በሌላ ስሙ የማደሪያ ድንኳን ተብሎ ይታወቃል (ዘጸአት 27፡21 ተመልከት)

Exodus 29:5

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• ሸሚዝ

ባጌጠ ጥልፍ የተሰራና በእፉዱ ላይ በውጭ በኩል የሚለበስ ልብስ ወይም ኮት። ነገር ግን እንደ ዛሬው የሸሚዝ ዓይነት ከጃኬት ወይም ከኮት ሥር የሚለበስ አይደለም (ዘጸአት 28፡4 ተመልከት)

• በብልሃትም በተጠለፈ ቋድ

ይህ ከቀጭን የሐር ልብስ/ጨርቅ/ክር/ ተገምዶ የተሰራ የወገብ ወይም በደረት አከባቢ የሚያደርጉት መታጠቂያ ነው (ዘጸአት 28፡8 ተመልከት)

• መጠምጠሚያ

አንድ ሰው ወይም ካህኑ በራሱ ላይ ዙሪያውን የሚጠመጥመው ራስ መሸፈኛ ነው (ዘጸአት 28፡4 ተመልከት)

• የተቀደሰ አክሊል

በዚህ ክፍል የተጠቀሰው “አክሊል” በጠፍጣፋ/ዝርግ/ ወርቅ ላይ “ቅድስና ለእግዚአብሔር” ወይም “ለእግዚአብሔር የተለየ” ተብሎ የተቀረጸውን የሚመለከት ነው። ይህ ጠፍጣፋ/ዝርግ/ ወርቅ ከራስ መጠምጠሚያው ላይ የተሰፋ ወይም የተያያዘ ነበር።

Exodus 29:8

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• ልጆቹንም ታቀርባቸዋለህ

የአሮን ልጆች ወደ አንተ ታመጣቸዋል/ታቀርባቸዋለህ/

• ሸሚዞቹንም ታለብሳቸዋለህ

ባጌጠ ጥልፍ የተሰራና በእፉዱ ላይ በውጭ በኩል የሚለበስ ልብስ ወይም ኮት። ነገር ግን እንደ ዛሬው የሸሚዝ ዓይነት ከጃኬት ወይም ከኮት ሥር የሚለበስ አይደለም። በሌላ አገላለጽ፦ ሸሚዝ/ኮት/ አልብሳቸው (ዘጸአት 28፡4)

• መታጠቂያ

ይህ ከቀጭን የሐር ልብስ/ጨርቅ/ክር/ ተገምዶ የተሰራ የወገብ ወይም በደረት አከባቢ የሚያደርጉት መታጠቂያ ነው (ዘጸአት 28፡4 ተመልከት)

• ቆብንም ታለብሳቸዋለህ

በራስ/በጭንቅላት/ ላይ የሚደረግ/የሚለበስ/ ውበት ያለው ከልብስ/ከጨርቅ/ የተሰራ ጥብቅ ጥምጥም

• ክህነት ይሆንላቸዋል

የክህነት አገልግሎታቸው/ሥራቸው/ተግባራቸው/

• ለዘላለም ሥርዓትም

ለዘለዓለም ቋሚ ሥርዓት ይሆናል (ዘጸአት 28፡43 ተመልከት)

Exodus 29:10

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• መገናኛው ድንኳን

በሌላ ስሙ የማደሪያ ድንኳን ተብሎ ይታወቃል (ዘጸአት 27፡21 ተመልከት)

• ወይፈኑን . . . ታርደዋለህ

ወይፈኑን/ወጣት በሬውን/ የሚያርደው ሙሴ እንጂ አሮን ወይም ካህናቱ አይደሉም። ወይፈኑ የሚታረደው በድንኳኑ በራፍ/ደጃፍ/ ላይ እንጂ ውስጥ አይደለም።

• ከወይፈኑም ደም ወስደህ

ከታረደው ወይፈን ደም ወስደህ

Exodus 29:12

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር(ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• መሠዊያው ቀንዶች ላይ

በመሰዊያው አራቱም ማእዘን ጫፍ ላይ ቀንድ መሳይ ጒጦች ላይ (ዘጸአት 27፡2)

• ደሙንም ሁሉ ከመሠዊያው በታች ታፈስሰዋለህ

የቀረውን /የተረፈውን/ ደም በመሠዊያው ሥር አፍስሰው

• የሆድ ዕቃውንም የሚሸፍነውን ስብ

የሆድ ዕቃውን /ውስጠኛውን ሆድ ዕቃ/ የሚሸፍነውን ሞራ/ስብ/

• የወይፈኑን ሥጋ ግን፥ ቁርበቱንም፥ ፈርሱንም ከሰፈር ውጭ በእሳት ታቃጥለዋለህ፣ የኃጢአት መሥዋዕት ነው

ነገር ግን የተረፈውን የኰርማውን ሥጋ፥ ቆዳውን፥ አንጀቱን ሁሉ ወስደህ ከሰፈር ውጪ አቃጥለው፤ ይህ የኃጢአት መሥዋዕት ነው

Exodus 29:15

• አውራውንም በግ ታርደዋለህ

ይህ አውራ በግ የሚታረደው ካህናትን ለማንጻት ነው፤ በጉን የሚያርደው አሮን ወይም የእርሱ ልጆች ሳይሆኑ ሙሴ ነው።

• አውራውን በግ በመሠዊያው ላይ ታቃጥላለህ

የወይፈኑ መስዋዕት ከሰፈር ውጪ ወይም ከመገናኛው ድንኳን ደጅ ላይ ታርዷል ነገር ግን አውራ በጉ በሰፈር ውስጥ ወይም በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ይታረዳል።

Exodus 29:19

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

Exodus 29:21

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• እርሱም ልብሶቹም፥ ከእርሱም ጋር ልጆቹ ልብሶቻቸውም ይቀደሳሉ

በዚህ ዐይነት እርሱ፥ ልጆቹ እና ልብሶቻቸው ጭምር ለእኔ የተለዩ ይሆናሉ

• የውስጥ ዕቃውን . . . ጉበቱን. . . ኩላሊቱን

እነዚህ የበግ፥ የፍየል፥ የከብት፥ ወዘተ ውስጠኛው የሰውነት ክፍል አካላት ናቸው

• በእግዚአብሔር ፊት በሌማት ካለው ቂጣ እንጀራ ትወስዳለህ

በመሶብ/በቅርጫት/ ካለው ለእኔ ለእግዚአብሔር ከቀረበው ቂጣ ከየአንዳንዱ ዐይነት አንድ ሙልሙል/ክብ/ ዳቦ ውሰድ (ዘጸአት 29፡2)

• በእግዚአብሔር ፊት

አንተ በእግዚአብሔር ፊት ካስቀምጥከው

Exodus 29:22

አጠቃላይ ዕይታ፦

ዕይታ፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

Exodus 29:24

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• ሁሉንም በአሮን እጆችና በልጆቹ እጆች ታኖረዋለህ

“ሁሉንም” የተባለው ቀደም ባሉት ቁጥሮች የተዘረዘሩትን የመስዋዕት ዓይነቶችን ማለቱ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “ይህን ሁሉ ምግብ በአሮንና በልጆቹ እጅ ላይ አኑር/አስቀምጥ/

• እርሱ ለእግዚአብሔር የእሳት ቍርባን ነው

ይህም በእሳት የሚቃጠል መስዋዕት ሆኖ ለእግዚአብሔር ይቀርባል/ይሰዋል/

Exodus 29:26

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• ለአሮንም ክህነት የታረደውን በግ

አሮንን ለክህነት አገልግሎት ለመሾም ከታረደው የበግ ጠቦት

• ከሚካኑበትም አውራ በግ

አሮንና ልጆቹ ከሚካኑበት /ለእግዚአብሔር ከሚለዩበት/ የበግ ጠቦት

• ለዘላለም የአሮንና የልጆቹ ወግ ይሁን

ለአሮንና ለልጆቹ ቋሚ ሥርዓት ይሁን

Exodus 29:29

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• የተቀደሰውም የአሮን ልብስ ይቀቡበትና ይካኑበት ዘንድ

እነርሱም (ልጆቹ) ተቀብተው የክህነት ሹመት/ሥልጣን/ በሚቀበሉበት ጊዜ ይልበሱት

• ከእርሱ በኋላ ለልጆቹ ይሁን

እነዚህ ልብሶች ተራ ልብሶች ወይም ደግሞ የአሮን የግሉ ልብሶች ሳይሆኑ የክህነት ልብሶች ናቸው። አማራጭ ትርጉም፦ አሮን በሚሞትበት ጊዜ የክህነት ልብሶቹ ለልጆቹ መተላለፍ አለባቸው፤

• መገናኛው ድንኳን

በሌላ ስሙ የማደሪያ ድንኳን ተብሎ ይታወቃል (ዘጸአት 27፡21 ተመልከት)

Exodus 29:31

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• የሚካንበትንም አውራ

ለካህናት የአገልግሎት ሹመት/ሥልጣን/ በምትሰጥበት ጊዜ የታረደው የበግ ጠቦት

• በተቀደሰ ስፍራ ትቀቅለዋለህ

ይህ ቦታ ከቅድስተ ቅዱሳን ወጭ ያለው ቅዱስ ስፍራ የሚመለከት አይደለም። ነገር ግን በመገናኛው ደንኳን አደባባይ ላይ ያለውን ሥፍራ የሚመለከት ነው።

• መገናኛው ድንኳን

በሌላ ስሙ የማደሪያ ድንኳን ተብሎ ይታወቃል (ዘጸአት 27፡21 ተመልከት)

• ሌላ ሰው ግን አይብላው

በሌላ አገላለጽ፦ ከካህናት ሌላ ማንም ሰው አይብላው

• የተቀደሰ ነውና

በሌላ አገላለጽ፦ ምክንያቱም የተቀደሰ ወይም ለእግዚአብሔር የተለየ ነው

Exodus 29:35

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• እንዳዘዝሁህም ሁሉ በአሮንና በልጆቹ እንዲህ አድርግ

አሮንና ልጆቹ ለክህነት አገልግሎት ስትሾም ወይም ሥልጣን ስትሰጥ ልክ እኔ ባዘዝኩህ ሥርዓት መሠረት ፈጽም

• መሠዊያውም ቅድስተ ቅዱሳን ይሆናል

በዚህም ዐይነት መሠዊያው ፍጹም የተቀደሰ ወይም ለእግዚአብሔር የተለየ ይሆናል

Exodus 29:38

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• በቀን በቀን ዘወትር ሁለት የዓመት ጠቦቶች ታቀርባለህ

በየዕለቱ አንድ ዓመት የሆናቸውን ሁለት ጠቦቶች መሥዋዕት አድርገህ በመሠዊያው ላይ አቅርብ፤

Exodus 29:40

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• አራተኛ እጅ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች)

አንድ አራተኛ (¼) ማለት ነው

• አሥረኛ እጅ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች)

አንድ አስረኛ (1/10) ማለት ነው

• የኢን መስፈሪያ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች)

አንድ ኢን ወደ 3.7 ሊትር ያህል ነው

• የኢፍ መስፈሪያ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች)

አንድ ኢፍ ወደ 22 ሊትር ያህል የሚመዝን ነው

Exodus 29:41

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽቱ እንዲሆን የእሳት ቍርባን ይሆናል

ይህ ለእኔ ለእግዚአብሔር የሚቀርብ መዓዛው ደስ የሚያሰኝ የምግብ መባ/መስዋዕት/ ነው፤

• ለሚመጡት ዘመናት ሁሉ

ይህ ዘወትር ለልጅ ልጃችሁ ወይም በየዓመቱ የሚፈጸም

• መገናኛው ድንኳን

በሌላ ስሙ የማደሪያ ድንኳን ተብሎ ይታወቃል

Exodus 29:43

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

• ድንኳኑም በክብሬ ይቀደሳል

በሌላ አገላለጽ፦ ክብሬ ወይም ሕሊዎቴ ይህን ስፍራ የተቀደሰ ወይም የተለየ ያደርገዋል

Exodus 29:45

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል


Chapter 30

1 ዕጣን የሚጤስበት መሠዊያ ከግራር ዕንጨት ሥራ። 2 እርዝመቱ አንድ ክንድ፣ ወርዱም አንድ ክንድ ይሁን። አራት ማእዘንና ሁለት ክንድ ከፍታ ይኑረው። ቀንዶቹ ከመሠዊያው ጋር ወጥ ይሁኑ። 3 የዕጣን መሠዊያውን ላይኛ ክፍል፣ ጎኖቹንና ቀንዶቹን በንጹሕ ወርቅ ለብጣቸው። የመሠዊያውን ዙሪያ በወርቅ ክፈፈው። 4 ከክፈፉ በታች በሁለቱ ትይዩ ጎኖቹ ላይ እንዲያያዙ ሁለት የወርቅ ቀለበቶችን አብጅ። ቀለበቶቹ መሠዊያውን ለመሸከም መሎጊያዎችን ደግፈው የሚይዙ ናቸው። 5 ከግራር ዕንጨት ሥራና በወርቅ ለብጣቸው። 6 የዕጣን መሠዊያውን ከመጋረጃው ፊት በምስክሩ ታቦታ አጠገብ አስቀምጠው። ይህም እኔ ከአንተ ጋር በምገናኝበት፣ በምስክሩ ታቦታ ላይ ካለው ከስርየት መክደኛው ፊት ይሆናል። 7 ደስ የሚያሰኝ መዐዛ ያለውን ዕጣን ሁልጊዜ ጧት ቷት ያጢስ። ማጤስ ያለበትም መብራቶቹን በሚያዘጋጅበት ጊዜ ነው። 8 መብራቶቹን በምሽት ሲያበራም፣ በዕጣን መሠዊያው ላይ ዕጣን ማጤስ አለበት። ይህ በእኔ በእግዚአብሔር ፊት ዘወትር በትውልዶች ሁሉ የሚጤስ ዕጣን ይሆናል። 9 ነገር ግን ሌላ ዕጣን፣ አንዳችም የሚቃጠል መሥዋዕት ወይም የእህል ቍርባን በዕጣን መሠዊያው ላይ አታቅርብ፤ ምንም ዐይነት የመጠጥ ቍርባንም አታፍስስበት። 10 መሠዊያው ቀንዶች ላይ አሮን በዓመት አንድ ጊዜ ማስተስረያ ያድርግ ይህንም የሚያደርገው የኀጢአት ስርየት ደሙን በመጠቀም ነው። ሊቀ ካህናቱ በትውልዶቻችሁ ሁሉ ይህን ያድርገው። ይህ መሥዋዕት ሙሉ በሙሉ ለእኔ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ይሆናል።” 11 ሙሴን እንዲህ አለው፤ 12 ስትቆጥራቸው፣ እያንዳንዱ ሰው ለራሱ ሕይወት ቤዛ ለእግዚአብሔር መክፈል አለበት። ስትቆጥራቸውና ከቆጠርሃቸውም በኋላ በመካከላቸው መቅሠፍት እንዳይኖር ይህን አድርግ። 13 የተመዘገበ እያንዳንዱ ሰው በመቅደሱ ሰቅል ክብደት መሠረት የብር ግማሽ ሰቅል ይክፈል። ይህ ግማሽ ሰቅልም ለእኔ ለእግዚአብሔር የሚቀርብ መሥዋዕት ይሆናል። 14 ከሃያ እና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያለው የተቆጠረ ሁሉ ይህን መሥዋዕት ለእኔ ማቅረብ አለበት። 15 ለሕይወታቸው ማስተስረያ ለማድረግ ይህን መሥዋዕት ለእኔ ሲያቀርቡ፣ ባለጠጋው ከግማሽ ሰቅል የበለጠ፣ ድኻውም ከዚያ ያነሰ መስጠት የለባቸውም። 16 የማስተስረያ ገንዘብ ከእስራኤላውያን ተቀበልና ለመገናኛ ድንኳኑ ሥራ አውለው። ለሕይወታችሁ ማስተስረያ ማድረግ በፊቴ ለእስራኤላውያን መታሰቢያ ይሁን።” 17 ሙሴን እንዲህ አለው፤ 18 ትልቅ የናስ ሳሕን ከናስ መቆሚያ ጋር አብጅ። በመገናኛው ድንኳንና በመሠዊያው መካከል አስቀምጠውና ውሀ አድርግበት። 19 ልጆቹ እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ውስጡ ባለው ውሀ ይታጠቡ። 20 መገናኛው ድንኳን ሲገቡ ወይም የሚቃጠል መሥዋዕት በማቅረብ እኔን ለማገልገል ወደ መሠዊያው ሲቀርቡ፣ እንዳይሞቱ በውሀ መታጠብ አለባቸው። 21 እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ሊታጠቡ ይገባል። ይህ ለአሮንና ለዘሮቹ በትውልዶቻቸው ሁሉ የሁልጊዜ ሕግ ይሁን።” 22 ሙሴን እንዲህ አለው፤ 23 ምርጥ ቅመሞች፦ ዐምስት መቶ ሰቅል ፈሳሽ ከርቤ፣ ሁለት መቶ ዐምሳ ሰቅል ጣፋጭ ሽታ ያለው ቀረፋ፣ ሁለት መቶ ዐምሳ ሰቅል ጠጅ ሣር፣ 24 ዐምስት መቶ ሰቅል ብርጕድ በመቅደሱ ሰቅል ክብደት ተለክቶ፣ አንድ የኢን መስፈሪያ ወይራ ዘይትም ውሰድ። 25 ቅመሞች በሽቶ ቀማሚ ሥራ የተቀደሰ መቅቢያ ዘይት አዘጋጅ። ይህ ለእኔ የተቀደሰ መቅቢያ ዘይት ይሆናል። 26 ዘይት የመገናኛውን ድንኳን፣ የምስክሩን ታቦትም፣ 27 ጠረጴዛውንና ዕቃውንም ሁሉ፣ መቅረዙንና ዕቃውን፣ የዕጣን መሠዊያውንም፣ 28 የሚቃጠል መሥዋዕት ማቅረቢያ መሠዊያውን ከዕቃው ሁሉ ጋር፣ መታጠቢያ ሳሕኑንም ከመቆፕሚያው ጋር ቅባ። 29 ለእኔ የተቀደሱ እንዲሆኑ እነርሱን ለይልኝ። እነርሱን የሚነካ ማንኛውም ነገርም የተቀደሰ ይሆናል። 30 ሆነው እንዲያገለግሉኝ አሮንንና ልጆቹን ቅባቸው፣ ለእኔም ለያቸው። 31 እንዲህ በላቸው፤ ‘ይህ በትውልዶቻችሁ ሁሉ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ መቅቢያ ዘይት መሆን አለበት። 32 የሰው ቆዳ ሊቀባበት አይገባም፤ እንደዚህ ያለ አንዳችም ዘይት በአንድ ዐይነት ቀመር መሥራት የለባችሁም ምክንያቱም ይህ ዘይት ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ዘይት ነው። እናንተም ቅዱስ መሆኑን ዐስቡ። 33 እንደዚህ የሚሠራ ሁሉ፣ ወይም ከዚህ ዘይት ጥቂት በሰው ላይ የሚያፈስስ ሁሉ፣ ከወገኑ ይወገድ።’” 34 ሙሴን እንዲህ አለው፤ “የጣፋጭ ሽቶ ቅመሞችን፦ የሚንጠባጠብ ሙጫ፣ በዛጎል ውስጥ ያለ ሽቶ፣ የሚሸት ሙጫ ከንጹሕ ዕጣን ጋር፣ እያንዳንዱን በእኩል መጠን ውሰድ፥ 35 በሽቶ ቀማሚ እንደ ተሠራ፣ በጨው የተቀመመ፣ ንጹሕና ለእኔ የተቀደሰ ዕጣን አድርገው። 36 አድቅቀህ ትወቅጠዋለህ። ከፊሉን ከአንተ ጋር በምገናኝበት፣ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ባለው በምስክሩ ታቦት ፊት ለፊት አስቀምጥ። ለእኔ የተቄደሰ መሆኑንም ዐስብ። 37 እንደምትዘጋጀው ዕጣን በአንድ ዐይነት ቀመር ለራስህ ምንም አታድርግ። ለአንተ እጅግ ቅዱስ ይሁን። 38 እንደ ሽቶ ለመጠቀም እንደዚህ አድርጎ የሚሠራ ሁሉ ከገዛ ወገኑ ይወገድ።”



Exodus 30:1

አጠቃላይ ምልከታ፦

የአምልኮ ዕቃዎችን እንዴት መሥራት እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይነግረዋል።

• ቀንዶቹም ከእርሱ ጋር በአንድነት የተሠሩ ይሁኑ

በመሰዊያው አራቱም ማእዘን ጫፍ ላይ ቀንድ መሳይ ጒጦች ከመሰዊያው ጋር አንድ ወጥ ሆነው ይሰሩ

Exodus 30:3

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• ለመሸከምም የመሎጊያዎች ስፍራ ይሁኑ

ለመሸከም የሚያገለግሉት መሎጊያዎች እንዲገቡበት ከክፈፉ ሥር አያይዛቸው

Exodus 30:5

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• በምስክሩ ታቦት

የቃል ኪዳን ታቦት ሲሆን በድንጋይ ጽላት ላይ የተጻፉት ቃላት እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ለገባው ቃል ኪዳን ምስክር እንዲሆን ነው (ዘጸአት 26፡33 ተመልከት)።

• የስርየት መክደኛ

በምስክሩ ታቦት ላይ የሚቀመጥና የስርየት መስዋዕቱን የሚሸፍን መክደኛ ነው

• ይህንም አንተን በምገናኝበት

እኔም በዚያ ለአንተ እገለጥልሃለሁ ወይም እኔም ከአንተ ጋር እዚያ እገናኛለሁ

Exodus 30:7

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• በእግዚአብሔር ፊት ለልጅ ልጃችሁ

በእግዚአብሔር ፊት በሚመጡት ዘመናት ሁሉ ወይም በህሊዎተ እግዚአብሔር ፊት በሚመጡት ዘመናት

• አሮን በማታ ጊዜ መብራቶቹን ሲያበራ ያጥነዋል

ይህ ትዕዛዝ በሙሴ በኩል ለአሮን የተሰጠ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ አሮን በየምሽቱ መብራቶቹን ሲያበራ እንዲሁ ያድርገዋል።

Exodus 30:10

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል።

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል።

• በቀንዶቹ ላይ

በመሰዊያው አራቱም ማእዘን ጫፍ ላይ ቀንድ መሳይ ጒጦች ላይ

• ለልጅ ልጃችሁ

በሚመጡት ዘመናት ወይም ጊዜያት ሁሉ

Exodus 30:11

• አንተ የእስራኤልን ልጆች ቍጥር ተቀብለህ

አንተ የእስራኤልን ሕዝብ በምትቈጥርበት ጊዜና በቆጠራው ወቅት

• ግማሽ ሰቅል እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን ይሰጣል

እያንዳንዱ ሰው በተቀደሰው ድንኳን በታወቀው ሚዛን ልክ ስድስት ግራም ብር ይክፈል፤ ግማሽ ሰቅል (½) ከ5.5 – 6 ግራም ይመዝናል።

• እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን

በጊዜው ወይም በዚያን ጊዜ ሁለት ዓይነት ሚዛን እንዳለ ይታወቃል፤ አንደኛ መደበኛ የሆነ መገበያያ ሰቅል ሲሆን ሌላኛው በቤተመቅደስ አገልግሎት የሚሰጥ ሰቅል ነው።

• ሰቅሉ ሀያ ኦቦሊ ነው

አንድ ሰቅል ሃያ ኦቦሊ ያህል ሲሆን በዘመናዊ ሚዛን ወደ 0.6 ግራም የሚመዝን ነው፤ ኦቦሊ ከሁሉም ትንሹ የክብደት መለኪያ ነው።

• ከሀያ አመት ጀምሮ ከዚያም ከፍ ያለ

ሃያ ዓመት የሞላውና ከዚያም በላይ የሆነ ሁሉ

Exodus 30:15

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል።

• ከእስራኤል ልጆች

ከወንድ እስራኤላውያን ብቻ

• ግማሽ ሰቅል

ተርጓሚዎች የክብደት፥ የርዝመት፥ የፈሳሽና ሌሎችን መለኪያችን ስተረጉሙ ህብረተሰቡ በሚረዳው መለኪያ ብጠቀሙ መልካም ነው። ግማሽ ሰቅል ወደ 6 ግራም የሚመዝን ነው።

• በእግዚአብሔርም ፊት ለነፍሳችሁ ቤዛ እንዲሆን ለእስራኤል ልጆች መታሰቢያ ይሁን

ይህ አባባል የተለያየ ትርጉም ሊኖረው ይችላል፦ 1) እስራኤላውያን ለነፍሳቸው ወይም ለሕይወታቸው ቤዛ እንዲያቀርቡ ይህ ያሳስባቸዋል 2) እስራኤላውያን ለነፍሳቸው ወይም ለሕይወታቸው ቤዛ እንዳቀረቡ ያስገነዝባቸዋል። አማራጭ ትርጉም፦ ይህም መባ ለሕይወታቸው ቤዛ ስለሚሆን እኔ እነርሱን እያስታወስኩ እጠብቃቸዋለሁ”

Exodus 30:17

• የመታጠቢያ ሰን

የመታጠቢያ ገንዳ ወይም ገበቴ። ይህ የመታጠቢያ ገንዳ ካህናት የሚታጠቡበትን ውሃ የሚያኖሩበት ነው

• መቀመጫውን

የመታጠቢያ ገንዳው መቀመጫ ወይም ማስቀመጫ

• መሠዊያው

የእንስሳት መስዋዕት ማቅረቢያ ቦታ

Exodus 30:19

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• አሮንና ልጆቹም እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ይታጠቡበታል

በዚህ ውሃ አሮንና ልጆቹ እጃቸውንና እግራቸውን ለመታጠብ ይገለገሉበታል

• ይህም ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ የዘላለም ሥርዓት ይሆንላቸዋል

ይህም ለእነርሱና ከእነርሱ በኋላ ለሚመጡ ዘሮቻቸው/ትውልዶቻቸው/ የዘለዓለም ሥርዓት ሆኖ ይኖራል

Exodus 30:22

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• ቅመም

ጥሩ ሽታና ጣዕም እንዲኖረው ከደረቀ ዕጽዋትና ዘር ተፈጭቶ የተሰራና ዘይት ወይም ምግብ የገባበት ዱቀት ነክ ነገር ነው (ዘጸአት 25፡6 ተመልከት)

• አምስት መቶ ሰቅል . . . ሁለት መቶ አምሳ ሰቅል . . . ሁለት መቶ አምሳ ሰቅል፥

አንድ ሰቅል 11 ግራም ሲሆን ተርጓሚዎች ማህበረሰቡ በየዕለቱ አገልግሎቱ የምጠቀምበትን መለኪያ መጠቀም የተሻለ ነው። 500 ሰቅል ----- 5.5 ኪሎ ግራም፤ 250 ሰቅል ---- 2.75 ኪሎ ግራም፤ 250 ሰቅል ---- 2.75 ኪሎ ግራም ሲሆን በጠቅላላው 11 ኪሎ ግራም ያህል ነው።

• ጣፋጭ ቀረፋ

ጣፋጭ ሽታ ያለው ቀረፋ (የቅመም ዓይነት)

• እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን

በጊዜው ወይም በዚያን ጊዜ ሁለት ዓይነት ሚዛን እንዳለ ይታወቃል፤ አንደኛው መደበኛ የሆነ መገበያያ ሰቅል ሲሆን ሌላኛው ለቤተመቅደስ አገልግሎት የሚሰጥ ሰቅል ነው።

Exodus 30:26

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል

• የምስክር ታቦት

የቃል ኪዳን ታቦት ሲሆን በድንጋይ ጽላት ላይ የተጻፉት ቃላት እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ለገባው ቃል ኪዳን ምስክር እንዲሆን ነው።

• ለሚቃጠል መሥዋዕት የሚሆነውን መሠዊያ

ለሚቃጠል መሥዋዕት የሚያገለግለውን መሠዊያ ወይም የሚቃጠል መስዋዕት የሚቀርብበት መሰዊያ

Exodus 30:29

አጠቃላይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ መናገሩን ቀጥሏል

• ሁሉንም ትቀድሳቸዋለህ

ሁሉንም ለእግዚአብሔር የተለየ አድርገህ ታስቀምጣቸዋለህ

• ይህ ለልጅ ልጃችሁ የተቀደሰ የቅብዓት ዘይት ይሁንልኝ

ይህ የተቀደሰ ወይም ለእግዚአብሔር የተለየው የቅባት ዘይት ለሚመጡት ዘመናት ሁሉ ለእኔ አገልግሎት ይሁን፤

Exodus 30:32

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• በሰው ሥጋ ላይ አይፍሰስ

ለእግዚአብሔር የተለየው ዘይት በማንኛውም ተራ ሰው ላይ አይፍሰስ ወይም የማንኛውንም ተራ ሰው ቆዳ/ሥጋ/ አይንካ፤

• እንደ እርሱ ያለውን የሚያደርግ ሰው

ይህን የመሰለ ቅባት የሚሠራ ወይም ከዚህ ቅባት ወስዶ ካህን ያልሆነውን ሰው የሚቀባ

• ከሕዝቡ ተለይቶ ይጥፋ (ዘይቤያዊ አነጋገር)

ይህ ሀረግ ወደ ሶስት የተለያዩ ፍቺዎች አሉት፤ 1) እኔ ይህን ሰው ከእስራኤላውያን እንደ አንዱ አድርጌ እቀበላቸዋለሁ 2) እስራኤላውያን ይህ ሰው ከመካከላቸው ያውጡ/ይለዩ/ 3) እስራኤላውያን ይህን ሰው መግደል አለበት

Exodus 30:34

• ጣፋጭ ሽቱ፥ የሚንጠባጠብ ሙጫ፥ በዛጎል ውስጥ የሚገኝ ሽቱ

ጣፋጭ ቅመሞች፥ የሚንጠባጠብ ፈሳሽነት ያለው ሙጫ፥ በዛጎል ውስጥ የሚገኝ ሽቱ

• የሚሸትትም ሙጫ፥ ጥሩም እጣን ውሰድ

ይህ አባባል ሁለት ፍቺዎች አሉት፦ 1) ሙሴ ጣፋጭ ሽቶ ለመስራት ሌላ ሰው እንደቀጠረ 2) ጣፋጭ ሽቶ እንደሚሰራ ሰው ሙሴ ራሱ ሽቶዎችን እንደሰራ፤ አማራጭ ትርጉም፦ “የሚሸት ሙጫና ጣፋጭ ሽታ ያለው ዕጣን ወስደህ”

• ከእርሱም ጥቂት ትወቅጣለህ

ከእርሱም ጥቂቱን ወስደህ በመውቀጥ

Exodus 30:37

አጠቃላይ ዕይታ፦

እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ በኩል መናገሩን ቀጥሏል

• እንደ እርሱ የተሠራ ዕጣን ለእናንተ አታድርጉ

በዚህ ዐይነት የምታደባልቁትን ዕጣን ለራሳችሁ መጠቀሚያ አታድርጉት

•በእናንተ ዘንድም ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ይሁን

በዚህ ዐይነት የምታደባልቁትን ዕጣን ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ወይም የተለየ አድርገህ አቅርብ

• እንደ እርሱ የሚያደርግ ሰው ከሕዝቡ ተለይቶ ይጥፋ

ይህ ሀረግ ወደ ሶስት የተለያዩ ፍቺዎች አሉት፤ 1) እኔ ይህን ሰው ከእስራኤላውያን እንደ አንዱ አድርጌ እቀበላቸዋለሁ 2) እስራኤላውያን ይህ ሰው ከመካከላቸው ያውጡ/ይለዩ/ 3) እስራኤላውያን ይህንን ሰው መግደል አለበት


Chapter 31

1 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ 2 “የሖር የልጅ ልጅ የሆነውን የኡሪን ልጅ ባስልኤልን ከይሁዳ ነገድ በስሙ ጠርቼዋለሁ። 3 ለሁሉም ዐይነት የእጅ ሞያ ጥበብን፣ ማስተዋልንንና ዕውቀትን እንዲሰጠው፣ ባስልኤልን በመንፈስ ሞልቼዋለሁ፤ 4 ይኸውም ጥበባዊ ሥራዎችን በወርቅ፣ በብርና በነሐስ እንዲሠራ፣ 5 ዐይነት የእጅ ሞያ ለማከናወንም ድንጋይ እንዲጠርብና ዕንጨትም እንዲቀርጽ ነው። 6 ከእርሱም በተጨማሪ የአሂሳሚክን ልጅ ኤልያብን ከዳን ነገድ መርጬዋለሁ። ያዘዝሁህንም ሁሉ እንዲሠሩ የእጅ ሞያ ዐዋቂዎች በሆኑት ልብ ውስጥ ብልኀትን አስቀምጫለሁ። 7 የመገናኛውን ድንኳን፣ የምስክሩን ታቦት፣ በታቦቱ ላይ ያለውን የስርየት መክደኛና የድንኳኑን ዕቃ ሁሉ፦ 8 ጠረጴዛውንና ዕቃውን፣ ንጹሑን መቅረዝ ከዕቃዎቹ ሁሉ ጋር፣ የዕጣኑን መሠዊያ: 9 የሚቃጠለውን መሥዋዕት መሠዊያ ከዕቃዎቹ ሁሉ ጋርና ትልቁን ሰን ከነመቆሚያው የሚያካትት ይሆናል። 10 የተሠሩትን ልብሶች፦ ካህናት ሆነው እንዲያገለግሉኝ ለእኔ የተለዩትን የካህኑን የአሮንንና የልጆቹን የተቀደሱ ልብሶችም ይጨምራል። 11 ዘይቱንና የመቅደሱን ጣፋጭ ዕጣንም ያካትታል። እነዚህ የእሥ ሞያ ዐዋቂዎች እነዚህን ሁሉ እኔ ባዘዝሁህ መሠረት ይሥሯችው።” 12 ሙሴን እንዲህ አለው፤ 13 “ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ንገራቸው፦ ‘የእግዚአብሔርን የሰንበት ቀኖች ጠብቁ፤ እናንተን ለራሱ የለያችሁ እርሱ እግዚአብሔር መሆኑን እንድታውቁ፣ ይህ በእርሱና በእናንተ መካከል በትውልዶቻችሁ ሁሉ ምልክት ነውና። 14 ስለዚህ ለእናንተ የተቀደሰ የእግዚአብሔር ሰንበት ነውና አክብሩት። ሰንበትን የሚያረክስ ሁሉ ይሞታል። በሰንበት የሚሠራም ከወገኑ ተነጥሎ ይጥፋ። 15 ስድስት ቀን ይሠራል፤ ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር ክብር የተጠበቀና የተቀደሰ የፍጹም ዕረፍት ሰንበትን ያክብሩ። 16 በትውልዶቻቸው ሁሉ ቋሚ ሕግ አድረገው ሰንበትን ሊያከብሩት ይገባል። 17 እግዚአብሔር በስድስት ቀን ሰማይንና ምድርን ፈጥሮ በሰባተኛው ቀን ዐርፎአልና፣ ሰንበት በእግዚአብሔርና በእስራኤላውያን መካከል ሁልጊዜ ምልክት ይሆናል።” 18 እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ ከሙሴ ጋር የሚያደርገውን ንግግር ከጨረሰ በኋላ፣ በገዛ እጁ የጻፈባቸውን የምስክሩን ሁለት የድጋይ ጽላት ለሙሴ ሰጠው።



Exodus 31:1

• ባስልኤልን በስሙ ጠርቼዋለሁ

ይህ “በስሙ ጠርቼዋለሁ” የሚለው ስሙን መጥራት ሳይሆን “ለሥራው ለይቼዋለው ወይም መርጬዋለሁ” ማለት ነው። የእብራይስጥ ስሙ “ብጻልኤል” ሲሆን አማርኛ ትርጉሞች “ባስልኤል” ብለውታል። አማራጭ ትርጉም፦ “እኔ ባስልኤን መርጬዋለሁ”

• የሆር የልጅ ልጅ፥ የኡሪ ልጅ----

የወንዶች ስም ሲሆን የባስልኤል አባትና አያት የሚመለክቱ ናቸው

Exodus 31:3

• የእዚአብሔርን መንፈስ ሞላሁበት (ዘይቤያዊ)

እግዚአብሔር (ያህዌ) በአንድ ፈሳሽ መያዣ ውስጥ መንፈሱን እንደሚሞላ ባስልኤልን እሞላዋለሁ እያለ ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ መንፈሴን ለባስልኤል ሰጥቼዋለሁ

• በሁሉም ዐይነት የእጅ ጥበብ ሥራ

ማንኛውም ዓይነት ሥራ የመሥራት ችሎታና ጥበብ

Exodus 31:6

• ለእጅ ጥበብ ዐዋቂዎች ሁሉ ብልሃትን ሰጥቻቸዋለሁ

የእጅ ጥበብ ሥራዎችን ሁሉ መስራት እንዲችሉ ታላቅ ችሎታ እንዲኖራቸው አድርጌአለሁ

• የመገናኛውን ድንኳን

እግዚአብሔር በሙሴ አማካይነት ከህዝቡ ጋር የሚገናኝበት ድንኳን ማለት ነው

• የምስክሩንም ታቦት

የቃል ኪዳኑ ታቦት

• የስርየት መክደኛ

በምስክሩ ታቦት ላይ የሚቀመጥና የስርየት መስዋዕቱን የሚሸፍን መክደኛ ነው

• የዕጣን መሠዊያውን

ዕጣን የሚሰዋበት ቦታ ወይም የሚቀርብበት ቦታ

• ለሚቃጠል መሥዋት የሚሆነውንም መሠዊያ

የሚቃጠል መስዋዕት ለእግዚአብሔር የሚቀርብበት ቦታ ወይም የሚሰዋበት ቦታ

• የነጻውን መቅረዝ

ከንጹህ ወርቅ የተሰራውን የወርቅ መቅረዝ ወይም የብርሃን ማስቀመጫ

Exodus 31:10

• ልብሰ ተክህኖ

በጥብቅ የተሰራ የሊኖ ልብስ ሲሆን ካህናት በክህነት አገልግሎት ወቅት የሚለብሱት ልብስ ነው

Exodus 31:12

• ሰንበቶቼን ፈጽሞ ጠብቁ

እግዚአብሔር በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን የሚነግራቸው የሰንበት ቀን በማክበር እርሱን እንድታዘዙ ነው።አማራጭ ትርጉም፦ “የሰንበት ቀን በማክበር እኔን መታዘዝ አለባችሁ”

• በእኔና በእናንተ ዘንድ ለልጅ ልጃችሁ ምልክት ነው

ከትውልድ እስከ ትውልድ ድረስ ወይም እስከ ልጅ ልጃችሁ ድረስ ምልክት ይሆናል

• እኔ የምቀድሳችሁ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቁ

እግዚአብሔር ለራሱ የለያችሁ ወይም የመረጣችሁ ሰዎች ናችሁ

• ለእናንተ ቅዱስ ነውና ሰንበትን ጠብቁ

የሰንበት ቀን ማክበር ቅዱስ ተግባር ስለሆነ ሰንበቴን አክብሩ

• የሚያረክሰውም ሰው

ሰንበትን ማክበር የማይፈልግ ወይም የሰንበት ቀን አክብሮት የሚሽር ሰው ወይም ትኩረት የማይሰጥና የሚንቅ ሰው

• ሁሉ ፈጽሞ ይገደል

በአድራጊ ግስ፦ ይህን ሰው ግደሉ ወይም ከመካከላችሁ አስወግዱ ወይም ይህ ሰው በሞት ይቀጣ

ከሕዝቡ መካከል ተለይቶ ይጥፋ

ይህ አባባል በተለያዩ መንገዶች ልተረጎም ይችላል

  1. እግዚአብሔር ይህን ሰው ከህዝቡ መካከል ይለየዋል ወይም እንደራሱ ህዝብ አይቆጥረውም
  2. እናንተ እስራኤላውያን ይህን ሰው ከመካከላችሁ ለዩ ወይም አስወግዱ
  3. እናንተ እስራኤላውያን ይህን ሰው ያለ ርህራሄ ግደሉት
• ሰባተኛው ቀን

ቀን 7 ወይም የሳምንቱ 7ኛ ቀን

Exodus 31:16

• ሰንበትን ይጠብቁ

እግዚአብሔር በሙሴ በኩል ለእስራኤላውያን የሚነግራቸው የሰንበት ቀን በማክበር እርሱን እንድታዘዙ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የሰንበት ቀን በማክበር እኔን መታዘዝ አለባችሁ

Exodus 31:18

• በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈባቸውን

እግዚአብሔር ራሱ የጻፋቸው ወይም እግዚአብሔር ራሱ በራሱ እጅ የጻፋቸው


Chapter 32

1 ከተራራው ሳይወርድ እንደ ዘገየ ሕዝቡ ሲመለከቱ፣ በአሮን ዙሪያ ተሰብስበው እንዲህ አሉት፤ “በፊታችን የሚሄድ ጣዖት ሥራልን። ከግብፅ ያወጣን ሙሴ ምን እንዳጋጠምው አናውቅም።” 2 እንዲህ አላቸው፤ “በሚስቶቻችሁ ጆሮዎች፣ በወንድና በሴት ልጆቻችሁ ጆሮዎችም ላይ ያሉ የወርቅ ቀለበቶችን አውልቁና ወደ እኔ እምጧቸው።” 3 ሁሉም በጆሮዎቻቸው ላይ ያሉ የወርቅ ቀለበቶችን አውልቀው ወደ አሮን አመጧቸው። 4 ወርቁን ከእነርሱ ተቀብሎ በማቅለጥ ቅርጽ ሰጠው፤ የጥጃ ምስልም አደረገው። ሕዝቡም፣ “እስራኤል፣ ይህ ከግብፅ ምድር ያወጣህ አምላክህ ነው” አሉ። 5 ይህን ባየው ጊዜ፣ በጥጃው ምስል ፊት መሠዊያ ሠራ፤ “ነገ ለእግዚአብሔር ክብር በዐል ይሆናል” ብሎም ዐወጀ። 6 ሕዝቡ በማግስቱ ማልደው በመነሣት የሚቃጠሉ መሥዋዕቶችንና የኅብረት መሥዋዕቶችን አቀረቡ። ሊበሉና ሊጠጡም ተቀመጡ፤ ለመዝፈንም ተነሡ። 7 ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ከግብፅ ያወጣሃቸው ሕዝብህ ራሳቸውን በክለዋልና ቶሎ ሂድ። 8 መንገድ ፈጥነው ወጥተዋል። ለራሳቸው የጥጃ ምስል ሠርተው ሰግደውለታል፤ መሥዋዕትም አቅርበውለታል። ‘እስራኤል፣ ከግብፅ ያወጣህ አምላክህ ይህ ነው ብለውም ተናግረዋል።’” 9 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ይህን ሕዝብ አይቼዋለሁ። ተመልከት፣ ዐንገተ ደንዳናዎች ናቸው። 10 በእነርሱ ላይ እንዲቀጣጠልና እንዳጠፋቸው ተወኝ። ከአንተም ታላቅ ሕዝብ አደርጋለሁ (አንተንም ለታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ) ።” 11 ግን አምላኩ እግዚአብሔር ዝም እንዲልለት ፈለገ፤ እንዲህም አለ፤ “እግዚአብሔር ሆይ፣ በታላቁ ኀይልና በኀያል እጅ ከግብፅ ባወጣሃው ሕዝብህ ላይ ቊጣህ ለምን ይቀጣጠላል? 12 ‘እግዚአብሔር በተራሮች ላይ ሊገድላቸውና ከገጸ ምድር ሊያጠፋቸው ዐስቦ ነው ያወጣቸው’ ለምን ይበሉ? ከሚነድደው ቊጣህ ተመለስ፤ በሕዝብህ ላይ ይህን ቊጣ ከማምጣትም ታገሥ። 13 ‘ዘራችሁን እንደ ሰማይ ከዋክብት አበዛዋለሁ፣ የተናገርሁትን ይህንም ምድር ሁሉ ለዘራችሁ እሰጠዋለሁ፤ የዘለዓለም ርስታቸው ይሆናል’ ያልሃቸውንና በራስህ የማልህላቸውን ባሪያዎችህ አብርሃምን፣ ይስሐቅንና እስራኤልን ዐስብ።” 14 ከዚያም እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ አመጣባቸዋለሁ ካለው ቊጣ ታገሠ። 15 ተመለሰ፤ የምስክሩን ሁለት ጽላት በእጁ ይዞ ከተራራው ወረደ። ጽላቱ በሁለቱም ጎኖቻቸው፣ በፊትም በኋላም ተጽፎባቸው ነበር። 16 የእግዚአብሔር ሥራ ነበር፤ በጽላቱ ላይ የተቀረጸው ጽሕፈትም የእግዚአብሔር ጽሕፈት ነበር። 17 ላይ የተቀረጸው ጽሕፈትም የእግዚአብሔር ጽሕፈት ነበር። 17 ኢያሱ የሕዝቡን ጫጫታ ሲሰማ፣ ሙሴን፣ “በሰፈር ውስጥ የጦርነት ድምፅ አለ” አለው። 18 ሙሴም “የድል አድራጊ ድምፅ አይደለም፤ ድል የተደረገ ሕዝብ ድምፅም አይደለም፤ የምሰማው የዘፈን ድምፅ ነው” ብሎ መለሰለት። 19 ወደ ሰፈሩ ሲቀርብ፣ ጥጃውንና የሚጨፍረውን ሕዝብ አይቶ በጣም ተናደደ። ጽላቱን ከእጁ ወርውሮ በተራራው ግርጌ ሰበራቸው። 20 ሠርተውት የነበረውን ጥጃም ወስዶ አቃጠለው፤ ዱቄት እስከሚሆን ድረስ በመፍጨትም በውሀ ውስጥ በተነው። ከዚያም የእስራኤል ሕዝብ እንዲጠጣው አደረገ። 21 “እንደዚህ ያለ ታላቅ ኀጢአት ያመጣህበት ይህ ሕዝብ ምን አድርጎህ ነው?” አለው። 22 እንዲህ ብሎ መለሰለት፤ “ጌታዬ ሆይ ቊጣህ አይንደድ። እነዚህ ሰዎች ለክፋት የተዘጋጁ እንደ ሆኑ ታውቃለህ። 23 እንደዚህ ብለውኛል፤ ‘በፊታችን የሚሄድ አምላክ አብጅልን። ከግብፅ ያወጣን ሰውየ ይህ ሙሴ ምን እንዳጋጠመው አናውቅም።’ 24 እኔም፣ ‘ወርቅ ያለው ሰው ሁሉ ያውልቀው’ አልኋቸው። እነርሱም ወርቁን ሰጡኝ። በእሳት ውስጥም ጣልሁትና ይህ ጥጃ ወጣ።” 25 መዘባበቻ እንዲሆኑ አሮን መረን ስለ ለቀቃቸው፣ ሕዝቡ ከቊጥጥር ውጭ መሆናቸውን ሙሴ አስተዋለ። 26 በሰፈሩ መግቢያ ቆሞ፣ “የእግዚአብሔር የሆነ ሁሉ ወደ እኔ ይምጣ” አለ። ሌዋውያን ሁሉ በሙሴ ዙሪያ ተሰበሰቡ። 27 ሌዋውያኑን እንዲህ አላቸው፤ “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ይህን ተናግሮአል፦ ‘እያንዳንዱ ሰይፉን በወገቡ ይታጠቅና በሰፈሩ ሁሉ ከበር እስከ በር ወደ ኋላና ወደ ፊት እየተመላለሰ ወንድሙን፣ ጓደኛውንና ጎረቤቱን ይግደል።’” 28 ሌዋውያኑ ሙሴ ያዘዘውን ፈጸሙ። በዚያ ቀን ከሕዝቡ ሦስት ሺሕ ያህል ሰዎች ሞቱ። 29 ሌዋውያኑን፣ “ዛሬ ከእናንተ እያንዳንዱ በልጁና በወንድሙ ላይ እርምጃ ስለ ወሰደ፣ ለእግዚአብሔር አገልግሎት ተቀድሳችኋል። ስለዚህም እግዚአብሔር ዛሬ ባርኳችኋል” አላቸው። 30 በማግስቱም ሙሴ ሕዝቡን፣ “ታላቅ ኀጢአት ሠርታችኋል። አሁን ወደ እግዚአብሔር እወጣለሁ። ምናልባት ለኀጢአታችሁ ማስተሰረያ ማድረግ እችል ይህናል” አላቸው። 31 ሙሴ ወደ እግዚአብሔር ተመልሶ ሄደ፤ እንዲህም አለ፤ “ወዮ! እነዚህ ስዎች ታላቅ ኀጢአት ሠርተዋል፤ ለራሳቸውም ከወርቅ ጣዖት አበጅተዋል። 32 ግን እባክህ ኀጢአታቸውን ይቅር በል፤ ይቅር የማትላቸው ከሆነ ግን ከጻፍኸው መጽሐፍ እኔን ደምስስልኝ።” 33 ሙሴን እንዲህ አለው፤ እኔን የበደለኝን ሁሉ ከመጽሐፌ እደመስሰዋለሁ። 34 ሂድ፤ ሕዝቡን ወደ ነገርኋችሁ ስፍራ ምራው። እነሆ፣ የእኔ መልአክ በፊትህ ይሄዳል። ሕዝቡን በምቀጣበት ቀን ግን ስለ ኀጢአታቸው እቀጣቸዋለሁ።” 35 አሮን በሠራው ጥጃ ስላደረጉት፣ እግዚአብሔር በሕቡ ላይ መቅሠፍት ላከባቸው።



Exodus 32:1

• እንደ ዘገየ ባዩ ጊዜ

ይህ በዘይቤያዊ አነጋገር የተገለጸ ሲሆን አንድ ሰው ወይም አንድ ነገር እንደተገለጠ ወይም እንደታዬ አድርጎ ተገልጿል። አማራጭ ትርጉም፡- “እንደ ዘገየ በተረዱ ወይም ባስተዋሉ ጊዜ”

• ወደ አሮን ተሰብስበው

አሮንን አንድ ጥያቄ ለመጠየቅና ለማስገደድ እንደ መጡ ያሳያል። አማራጭ ትርጉም፦ ወደ አሮን መጥተው ወይም ቀርበው

• በፊታችን የሚሄዱ

እኛን የሚመሩን ወይም መሪ ልሆኑን የሚችሉ

Exodus 32:3

• ሕዝቡም ሁሉ

ሙሴንና የሙሴን እግዚአብሔር የተቃወሙ ሰዎች ሁሉና እግዚአብሔር አምላካቸው እንዳይሆን ሙሴ መሪያቸው እንዳይሆን ያልፈለጉ ሰዎች ሁሉ ማለት ነው

• የወርቅ ቀለበቶች ሰብራችሁ አምጡልኝ

“ሰብራችሁ” የሚለውን ቃል አዲሱ መደበኛ ትርጉም “አውልቃችሁ” ብሎ ተርጉሟል። ነገር ግን ይህ ትርጉም ልል ነው። በዕብራይስጡ ለማለት የተፈለገው “የወርቅ ጉትቻዎቻችሁን ከጆሮአችሁ ሰብራችሁ አውጥታችሁ” የሚል ጠንካራ ቃል ወይም ግስ ይጠቀማል።

• በመቅረጫ ቀረጸው፥ ቀልጦ የተሠራ ጥጃም አደረገው

አሮን ወርቆችን በማቅለጫ አቅልጦ፥ በጥጃም መልክ ቀርጾ ጣኦት ሰራላቸው።

Exodus 32:5

• አሮንም ባየው ጊዜ

ይህ ግልጽ ያልሆነ አባባል ነውና ግልጽ ማድረግ አስፈላጊ ነው። አሮን የእስራኤል ህዝብ ያደረገውን ባየ ጊዜ ወይም አሮን የሰራውን የወርቅ ጥጃ ባየ ጊዜ በሚል መተርጎም ይቻላል።

• ሊዘፍኑም ተነሡ

በአማርኛችን የዚህ ሀረግ ትርጉም በጣም ተደብቋል። “ሊዘፍኑም ተነሡ” የሚለው ተራ ዘፈን ሳይሆን ከሰው ባህርይ የወጣ ተግባር ሲፈጽሙ ነበር። ከበሉና ከጠጡ በኋላ ራሳቸውን መቆጣጠር አቅቷቸው በሜዳ ላይ ይሰስኑ፥ ይዳሩና ይዘሙቱ ነበር። የእንስሳነት ባህርይ ተላብሰው ልቅ ወሲብ ይፈጽሙ ነበር ማለት ነው።

Exodus 32:7

• ካዘዝኋቸው መንገድ ፈጥነው ፈቀቅ አሉ

እግዚአብሔር ሙሴን ሲናገር እስራላውያን ካሳየኋቸው መንገድ ፈቀቅ ብለዋል ሲል አንድ መንገድ እግዚአብሔር አሳይቷቸው እነርሱ ግን ያንን መንገድ ትተው በሌላ መንገድ እንደሄዱ አድርጎ ያቀርባል። አማራጭ ትርጉም፦ እንድያደርጉ ያዘዝኳቸውን ትዕዛዛት አላደረጉም ወይም ትዕዛዜን ለምድረግ ፈቃደኛ አይደሉም

• ቀልጦ የተሠራ የጥጃ ምስል ለራሳቸው አደረጉ

ለራሳቸውም በጥጃ ምስል የተቀረጸ ጣዖትን ሠርተው ለእርሱ ሰገዱለት

Exodus 32:9

• እኔ ይህን ሕዝብ አየሁት (ዘይቤያዊ ንግግር)

እግዚአብሔር (ያህዌ) ይህን ህዝብ አውቃለሁ በማለት ፋንታ ይህን ህዝብ አየሁ ይላል። አማራጭ ትርጉም፦ ይህን ህዝብ አውቃለሁ

• አንገተ ደንዳና ሕዝብ ነው (ዘይቤያዊ ንግግር)

“አንገተ ደንዳና” የሚለው ሀረግ “ልቤ ደነዳና ወይም የማይታዘዝ ልብ” የሚለውን ትርጉም ይይዛል። ነገር ግን አማርኛው የልብን እልከኝነት በአንገተ ደንዳናነት ሲተካው እናያለን።

• አሁንም

እግዚአብሔር (ያህዌ) ከሙሴ ጋር ሲያደርግ የነበረው ንግግር ላይ ሌላ አዲስ የንግግር ምዕራፍ ሲከፍት እናያለን፥ ስለሆነም ያህዌ ሊያደርግ ያለውን ነገር ለሙሴ ሲናገር እናያለን።

• ቁጣዬ እንዲቃጠልባቸው እንዳጠፋቸውም ተወኝ

እግዚአብሔር (ያህዌ) ቁጣው እንደ እሳት ትኩስና የሚያቃጥል እንደሆነ ይናገራል። አማራጭ ትርጉም፦ በእነርሱ ላይ እጅግ ተቈጥቼ ላጠፋቸው ስለ ተዘጋጀሁ ተወኝ

• አንተንም ለታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ

“አንተን” የተባለው ሙሴ ሲሆን በተውላጠ ስም ተጠቅሷል።

• ቁጣህ በታላቅ ኃይልና በጽኑ እጅ ከግብፅ ምድር ባወጣኸው በሕዝብህ ላይ ስለ ምን ተቃጠለ? (አጋናኝ ጥያቄ)

ሙሴ ይህን ጥያቄ እግዚአብሔርን (ያህዌን) የጠየቀው እግዚአብሔር በህዝቡ ላይ እንዳይቆጣ ለመለመን ወይም ለማሳመን ነው። ይህ አጋናኝ ጥያቄ በመደበኛ ዐረፍተ ነገር ሲተረጎም፦ እግዚአብሔር ሆይ፥ በሥልጣንህና በታላቅ ኀይልህ ከግብጽ ምድር ያወጣኸውን ሕዝብህን አትቆጣ

• በታላቅ ኃይልና በጽኑ እጅ

ሁለቱ ሀረጎች ተመሳሳይ ፍቺ የሚጋሩ ሲሆን ለንግግሩ አጽንኦት ለመስጠት የገቡ ናቸው።

• በጽኑ እጅ

“ጽኑ እጅ” የሚያመለክተው ከዚህ በፊት እስራኤላውያንን ከግብጽ ለማውጣት እግዚአብሔር የሰራቸውን ሥራዎች የሚያመለክት ነው።

Exodus 32:12

እግዚአብሔር እስራኤላውያንን እንዳያጠፋቸው እግዚአብሔር ምክንያት እየሰጠ ንግግሩን ይቀጥላል።

እግዚአብሔር እስራኤላውያንን እንዳያጠፋቸው እግዚአብሔር ምክንያት እየሰጠ ንግግሩን ይቀጥላል።

• ግብፃውያንስ፦ በተራራ መካከል ሊገድላቸው፥ ከምድርም ፊት ሊያጠፋቸው ለክፋት አወጣቸው ብለው ስለ ምን ይናገራሉ? (አጋናኝ ጥያቄ)

ይህ አጋናኝ ጥያቄ የሚያመለክተው እስራኤላውያንን እንዳያጠፋቸው ሙሴ እግዚአብሔርን ሲለምን የሚያሳይ ነው። አማራጭ ትርጉም ግብጻውያን ‘እግዚአብሔር ከግብጽ ምድር መርቶ ያወጣቸው በተራራዎች ላይ ሊገድላቸውና ፈጽሞ ሊያጠፋቸውና ለክፉ ነግር ነው’

• ከምድር ፊት

ከምድር ላይ

• ከመዓትህ ተመለስ

ከክፉ ቍጣህ ተመለስ ወይም ሀይለኛ ቁጣህን ተው

• አብርሃምንና ይስሐቅን እስራኤልንም፥ አስብ

አብርሃምን፥ ይስሃቅንና ያዕቆብን (እስራኤልን) አስታውስ

• የማልህላቸውን

ቃል ኪዳን የገባህላቸውን

• ለዘላለምም ይወርሱአታል

ለዘላለምም ይወርሱአታል ወይም የራሳቸው አድርገው ይይዟታል

Exodus 32:15

• ሁለቱንም የምስክር ጽላቶች

በሁለት ጠፍጣፋ ድንጋዮች ላይ የተጻፉ የእግዚአብሔር ትዕዛዛት /ትዕዛዞች/

• እርሱም

ሙሴም

Exodus 32:19

• ጽላቶቹንም

እግዚአብሔር የጻፈባቸውን ሁለቱን ጠፍጣፋ ድንጋዮች

Exodus 32:21

• ይህን ታላቅ ኃጢአት ታመጣበት ዘንድ ይህ ሕዝብ ምን አደረገህ? (ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆነ ጥያቄ)

“ይህ ሕዝብ ምን አድርጎህ ወይም በድሎህ ነው ይህን የመሰለ ክፉ ኃጢአት እንዲሠራ ያደረግኸው?”

• ይህን ታላቅ ኃጢአት ታመጣበት ዘንድ

ሀጢአት እንደ አንድ ግዑዝ ነገር ሆኖ አሮን በህዝቡ ላይ እንዳመጣበት በዘይቤያዊ አነጋገር ሙሴ ይገልጸዋል። አማራጭ ትርጉም፦ ይህን ክፉ ሀጢአት እንዲሰሩ ምክንያት የሆንከው አሮን አንተ ነህ

• ጌታዬ ሆይ፥ ቁጣህ አይቃጠል (ዘይቤያዊ አነጋገር)

ጌታዬ በእኔ ላይ እንዲህ በሀይል አትቈጣ

• ይህ ሕዝብ ክፋትን እንዲወድድ አንተ ታውቃለህ (ዘይቤያዊ ንግግር)

ይህ ሕዝብ ምን ያህል የክፋት ዝንባሌ እንዳለው ወይም ክፉ የማድረግ ፍላጎት እንዳለው አንተ ታውቃለህ

• ይህ ከግብፅ ምድር ያወጣን ሰው ሙሴ

“ይህ ሙሴ” የሚለው ሀረግ ህዝቡ ለሙሴ ያለው አክብሮት እንደ ወረደባቸው የሚገልጽ ነው። ከዚህ በፊት ሙሴን እንደማያውቁና እርሱም የማይታመን ሰው እንደሆነ “ይህ ሙሴ” በሚለው ሀረግ አርቀው ይናገራሉ።

• እኔም፦ ከእናንተ ወርቅ ያለው ሰው ከእርሱ ሰብሮ ያምጣልኝ

እኔ የወርቅ ጉትቻዎቻቸውን ወይም ጌጣጌጦቻቸውን አውልቀው ወይም ሰብረው እንዲያመጡልኝ ነገርኳቸው

• በእሳትም ላይ ጣልሁት፥ ይህም ጥጃ ወጣ

አሮን ሀላፊነት የወርቅ ጥጃውን ስለመስራቱ ላለመውሰድ ሲፈልግ እኔ ወርቆቹን ወደ እሳት ጣልኩኝ ነገር ግን ይህ ጥጃ ወጣ ብሎ ሲያስተባብል እናያለን።

Exodus 32:25

• በጠላቶቻቸው ፊት እንዲነወሩ

ህዝቡ ነውረኛ ነገር በማድረግና ራሳቸውም ነውረኛ በመሆን ልቅ ተግባር ፈጽመዋል።

• በሰፈሩ ደጅ ቆሞ፦ የእግዚአብሔር ወገን የሆነ ወደ እኔ ይምጣ! (ቀጥተኛ ያልሆነ ንግግር)

ሙሴ ወደ ሰፈሩ መግቢያ በር/ደጅ/ ቆሞ የእግዚአብሔር ወገን የሆነ ሁሉ ወደ እርሱ እንድመጣ ለእስራኤላውያን ተናገረ።

• የእግዚአብሔር ወገን የሆነ

ለእግዚአብሔር ታማኝ የሆነ ሰው የእግዚአብሔር ወገን እንደሆነ በዘይቤያዊ ንግግር ቀርቧል። በሰፈሩም ውስጥ በዚህና በዚያ ከበር እስከ በር ተመላለሱ፤ የእናንተም ሰው ሁሉ ወንድሙን ወዳጁንም ጎረቤቱንም ይግደል በሰፈር ውስጥ ከአንዱ በር/ደጅ/ ወደ ሌላው በር/ደጅ/ እያለፈ ወይም እየዞረ እያንዳንዱ ሰው ወንድሙን፣ ጓደኛውንና ጎረቤቱን ይግደል።

Exodus 32:28

• ከሕዝቡ ሦስት ሺህ ሰዎች ሞቱ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቁጥሮች)

“3000 ሰው ሞተ”

• እጃችሁን ለእግዚአብሔር ቅዱስ አድርጉ

እግዚአብሔርን የምታገለግሉ ካህናት ሆናችሁ ራሳችሁን ቀድሳችኋል

• እያንዳንዳችሁ በልጃችሁና በወንድማችሁ ላይ

እግዚአብሔርን (ያህዌ) በመታዘዝ እያንዳንዳችሁ ልጆቻችሁንና ወንድሞቻችሁን ገድላችኋል

Exodus 32:30

• እናንተ ታላቅ ኃጢአት ሠርታችኋል

እናንተ ጣዖት በማምለክ እጅግ የከፋ ሀጢአት ሰርታችኋል

• ምናልባት ኃጢአታችሁን አስተሰርይላችኋለሁ

ሙሴ ወደ እግዚአብሔር በመለመን እግዚአብሔር ይቅር እንዲላቸው ልመና ለማቅረብ ሲዘጋጅ ይታያል። አማራጭ ትርጉም፦ ምናልባት ስለ ኃጢአታችሁ ይቅርታ አስገኝላችሁ ይሆናል

• እባክህ ደምስሰኝ

“እባክህ ደምስሰኝ” የሚለው ሙሴ ስለራሱ ሲናገር ያሳያል። አማራጭ ትርጉም፦ ይህ የማይሆን ከሆነ ወይም ይቅር የማትላቸው ከሆነ የእኔን ስም ሰርዝ

• ከጻፍኸው መጽሐፍህ

የሕዝብህ ስሞች ከተጻፉበት መዝገብ

Exodus 32:33

• እርሱን ከመጽሐፌ እደመስሰዋለሁ

“እርሱን” የሚለው ያንን ሀጢአት የሰራውን ሰው ስም ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔን የበደለኝን ሰው ስም ከመጽሐፌ እሰርዛለሁ

• ከመጽሐፌ

ይህ መጽሐፍ ሙሴ የሚናገረው የእግዚአብሔር (ያህዌ) መጽሐፍ ነው። የመጽሐፉ ባለበት እግዚአብሔር (ያህዌ) ነው።

• ነገር ግን በምጐበኝበት ቀን ኃጢአታቸውን አመጣባቸዋለሁ አለው

ነገር ግን እኔ እነርሱን የምቀጣበት ጊዜ ሲደርስ ስለ ኀጢአታቸው የምቀጣው እኔ እግዚአብሔር ነኝ

• እግዚአብሔር ሕዝቡን ቀሠፈ

በምን ዓይነት ሁኔታ ህዝቡን እንደቀሰፈ አልተገለጸም ነገር ግን በበሽታ ሊሆን ይችላል። አማራጭ ትርጉም፦ እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ ከባድ በሽታ ላከ

• አሮን የሠራውን ጥጃ ስለ ሠሩ

የጥጃ ምስል ጣኦት የሰራው አሮን ቢሆንም ያንን የጥጃ ምስል ጣኦት አሮን እንዲሰራው ያስገደዱት ህዝቡ ነበሩ። አማራጭ ትርጉም፦ አሮን የጥጃ ምስል ጣኦት እንዲሰራ ህዝቡ በማስገደዳቸው


Chapter 33

1 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ “አንተና ከግብፅ ያወጣሃው ሕዝብ ከዚህ ሂድ። ‘ለዘርህ እሰጠዋለሁ’ ባልሁ ጊዜ፣ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ወደማልሁበት ምድር ሂድ። 2 በፊትህ መልአክ እሰድዳለሁ፤ ከነዓናውያንን፣ አሞራውያንን፣ ኬጤያውያንን፣ ፌርዛውያንን፣ ኤዊያውያንና ኢያቡሳውያንንም አስወጣቸዋለሁ። 3 ማርና ወተት ወደምታፈስሰዋ ምድር ሂዱ፤ ነግር ግን እናንተ ግትሮች ስለ ሆናችሁ፣ እኔ ከእናንተ ጋር አልወጣም። በመንገድ ላይ ላጠፋችሁ እችላለሁ።” 4 እነዚህን አስጨናቂ ቃሎች ሲሰሙ፣ አለቀሱ፤ ምንም ዐይነት ጌጥ ያደረገ ሰውም አልነበረም። 5 ሙሴን እንዲህ ብሎት ነበር፤ “ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ንገራቸው፤ ‘እናንተ ግትር ሰዎች ናችሁ። ለአፍታ እንኳ ዐብሬአችሁ ብሄድ፣ አጠፋችኋለሁ። ስለዚህ ምን እንደማደርግባችሁ ለመወሰን ጌጣጌጦቻችሁን አውልቁ።” 6 እስራኤላውያንም ከኮሬብ ተራራ ጀምረው ጌጦቻቸውን አወለቁ። 7 አንድ ድንኳን ወሰደና በተወሰነ ርቀት ላይ ከሰፈር ውጭ ተከለው። የመገናኛ ድንኳን ብሎ ጠራው። ስለ ማንኛውም ጕዳይ እግዚአብሔርን የሚጠይቅ ሰው ሁሉ ከሰፈሩ ውጭ ወደሚገኘው የመገናኛ ድንኳን ይሄድ ነበር። 8 ወደ ድንኳኑ ሲሄድ፣ ሕዝቡ ሁሉ በየድንኳኑ መግቢያ ላይ ቆሞ ወደ ድንኳኑ ሲገባ ሙሴን ይመለከት ነበር። 9 ወደ ድንኳኑ በሚገባበት ጊዜ ሁሉ፣ የደመና ዐምድ ይወርድና በድንኳኑ መግቢያ ላይ ይቆማል። እግዚአብሔርም ከሙሴ ጋር ይነጋገራል። 10 ሕዝቡ በድንኳኑ መግቢያ ላይ የደመናውን ዐምድ ቆሞ ሲያዩት፣ እያንዳንዱ ሰው በራሱ ድንኳን መግቢያ ላይ ይነሣና ይሰግዳል። 11 እግዚአብሔር አንድ ሰው ጓደኛውን እንደሚያነጋግር፣ ሙሴን ፊት ለፊት ያነጋግረዋል። ከዚያም በኋላ ሙሴ ወደ ሰፈሩ ይመለሳል፤ አገልጋዩና ወጣት የነበረው የነዌ ልጅ ኢያሱ ግን ከድንኳኑ አይለይም ነበር። 12 ሙሴ እግዚአብሔርን እንዲህ አለው፤ “ይህን ሕዝብ ምራው ብለኸኝ ነበር፤ ከእኔ ጋር ማንን እንደምትልክ ግን አላሳወቅኸኝም። ‘በስም ዐውቅሃለሁ፤ በፊቴም ሞገስ አግኝተሃል’ ብለሃል። 13 በፊትህ ሞገስ ካገኘሁ፣ እንዳውቅህና በፊትህ ሞገስን በማግኘት እንድቀጥል መንገዶችህን አሳየኝ። ይህ ሕዝብ የአንተ ሕዝብ እንደ ሆነም አስታውስ።” 14 እግዚአብሔርም መልሶ፣ “የእኔ ሀልዎት ከአንተ ጋር ዐብቶ ይሄዳል፤ ዕረፍትም እሰጥሃለሁ” አለው። 15 እግዚአብሔርን እንዲህ አለው፤ “የአንተ ሀልዎት ዐብሮን የማይሄድ ከሆነ፣ ከዚህ አታውጣን። 16 ከእኛ ጋር ካልሄድህ፣ እኔና ሕዝብህ በፊትህ ሞገስ ያገኘን መሆናችን እንዴት ሊታወቅ ይችላል? እኔና ሕዝብህ በምድር ገጽ ካለው ሕዝብ ሁሉ የተለየን የምንሆነው አንተ ከእኛ ጋር ብትሄድ ብቻ አይደለምን?” 17 ሙሴን፣ “በፊቴ ሞገስን ስላገኘህና በስምም ስለማውቅህ፣ የጠየቅኸውን አድረጋለሁ” አለው። 18 “እባክህ ክብርህን አሳየኝ” አለ። 19 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ አለው፤ “መልካምነቴ ሁሉ በፊትህ እንዲያልፍ አደርጋለሁ፤ ስሜን እግዚአብሔርንም በፊትህ ዐውጃለሁ። የምምረውን እምረዋለሁ፤ የምራራለትንም እራራለታለሁ።” 20 ነገር ግን እግዚአብሔር፣ ፊቴን ማየትና በሕይወት መኖር የሚችል ሰው ስለሌለ፣ አንተ የእኔን ፊት ማየት አትችልም” ብሎ መለሰለት። 21 እንዲህ አለ፤ “እነሆ፣ በእኔ ዘንድ ስፍራ አለ፤ አንተ በዚህ ዐለት ላይ ትቆማለህ። 22 ክብሬ በዚያ ሲያልፍ፣ እኔ እስከማልፍ ድረስ አንተን በዐለቱ ስንጥቅ ውስጥ በእጄ እሸፍንያለሁ። 23 ከዚያም እጁን አነሣውና ጀርባዬን ታያለህ፤ ፊቴ ግን አይታይም።”



Exodus 33:1

አጠቃላይ ምልከታ፦

ምልከታ፦ እግዚአብሔር (ያህዌ) በህዝቡ ላይ መቆጣቱን ቀጥሎ ይናገራል።

• ወተትና ማርም ወደምታፈስሰው ምድር

ይህ ሐረግ በግነታዊ እና በተለዋጭ ዘይቤ የተገለጸ ነው። ይህ አገላለጽ ከምድሪቱ ወተትና ማር ይፈልቃል ማለት ሳይሆን ለከብት እርባታና ለእርሻ በጣም ምቹ የሆነ ምድር እንደሆነ ለማሳየት ነው። እንዲሁም “የምታፈስ” አገር የሚለው ቃልም ሁሉም ነገር የሞላባት ምድር የሚል ፍቺ ያለው ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ለከብት እርባታና ለእርሻ ምቹ የሆነ ምድር

• ወተት

በእንስሳት ምርትና ተዋጽኦ የዳበረች አገር መሆኑዋን ለማመልከት ነው

• ማር

በእስራኤል ምድር ማር በሁለት መንገዶች ይመረታል። አንደኛው ከንብ እርባታ የሚገኘው ሲሆን ሁለተኛው ከተምር ዛፍና ከሌሎች ዕጽዋት የሚገኘው ነው።

• አንገተ ደንዳና ሕዝብ

ጸሐፊው የማይታዛዝ ህዝብ መሆኑን ለማሳየት በዘይቤያዊ አነጋገር ይገልጻል። የልባቸው እልከኝነት ከአንገት ደንዳናነት ጋር ተነጻጽሯል። አንገተ ዳንዳና ማለት ገታራና የማይመለስ ወይም መታጠፍ የማይችል ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ የማይሰማና የማይታዘዝ ህዝብ፤ ለለውጥ ያልተዘጋጀ ህዝብ ወይም ከገታራ አቋሙ የማይመለስ ማለት ነው።

Exodus 33:4

• ከእነርሱም ማንም ጌጡን አልለበሰም

ምንም ዐይነት ጌጣጌጥ (የጆሮ ጌጥ፥ የአንገት ሀብል፤ እና ሌሎች ጌጣጌጦች) ማድረግ አልፈለጉም

• እናንተ አንገተ ደንዳና ሕዝብ ናችሁ

እናንተ የማትታዘዙና የማትሰሙ ለለውጥም ያልተዘጋጃጅችሁ ሰዎች ናችሁ

Exodus 33:7

• የደመና ዓምድ

ደመናው እንደ አምድ ይታይ ነበር ወይም የአምድ ቅርጽ ነበረው ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “ደመናው በአምድ ቅርጽ ይወርድ ነበር”

• ይወርድ ነበር

የጋራ መረዳት ከለሌው ከየት እንደሚወርድ አይገልጽም። አማራጭ ትርጉም፦ “ከሰማይ ይመጣ ነበር”

Exodus 33:10

• እግዚአብሔር --- ፊት ለፊት ከሙሴ ጋር ይነጋገር (ዘይቤያዊ ንግግር)

በራዕይና በህልም ሳይሆን እግዚአብሔር በቀጥታ አንድ ሰው ከሌላ ሰው ጋር ፊት ለፊት ወይም አንዱ ሌላውን እያየ እንደምነጋገር ከሙሴ ጋር ይነጋገር። አማራጭ ትርጉም፦ “እግዚአብሔር (ያህዌ) ከሙሴ ጋር በቀጥታ ይነጋገር ነበር”

• ሎሌው ብላቴና

ኢያሱ ከሙሴ ይልቅ ወጥት ሲሆን “ብላቴና” የተባለው ወጣት መሆኑን ያሳያል፥ ሎሌው የተባለው “ረዳት” መሆኑን ይገልጻል። አማራጭ ትርጉም፦ “ረዳቱ ወጣት”

Exodus 33:12

• እነሆ

“እይ” ወይም “ስማ” ወይም “አድምጠኝ” እንደማለት ነው። ቃሉ በዕብራይስጥ ትኩረት ለመሳብ ወይም የሀሳብ አንድነት መኖሩን ለማመልከት የገባ ነው።

• በስምህ አወቅሁህ

አንድን ሰው በስም ማወቅ ያንን ሰው በሚገባ ወይም በትክክል እናውቄዋለን ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “እኔ አንተን በደንብ አውቅሃለሁ”

• በእኔ ፊት ሞገስን አገኘህ (ዘይቤያዊ አነጋገር)

በዚህ ሀረግ “ሞገስ አገኘህ” የሚለው የሚያመለክተው ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን ዕውቅና ያገኘ ወይም እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ ደስ ተሰኘ ማለት ነው። “እኔ ፊት” የተባለው በእግዚአብሔር እይታ ወይም የእግዚአብሔርን ግምገማ የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ አንተን ገምግሜ ዕውቅና ሰጥቼሃለሁ ወይም በአንተ ተደስቻለሁ/በአንተ ደስ ይለኛል/

• መንገድህን እባክህ አሳየኝ

ይህን ሀረግ በሁለት መልኩ መተርጎም ይቻላል፦ ወደፊት ማድረግ የምትፈልገውን ነገር እባክህ ንገረኝ ወይም ወደፊት ህዝቡ ማድረግ የሚገባቸውን ነገር እባክህ አሳያቸው

Exodus 33:14

• አሳርፍህማለሁ

ዕረፍት እሰጥሃለሁ

• በምን ይታወቃል? (አጋናኝ ጥያቄ)

ሰዎች ሁሉ እንዴት ሊያውቁ ይችላሉ?

Exodus 33:17

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር “አንተ’ እያለ በነጠላ ቁጥር የሚናገረው “ሙሴን” የሚመለከት ነው።

• በፊቴ ሞገስ ስላገኘህ

በዚህ ሀረግ “ሞገስ ስላገኘህ” የሚለው የሚያመለክተው ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን ዕውቅና ያገኘ ወይም እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ ደስ ተሰኘ ማለት ነው። “በፊቴ” የተባለው በእግዚአብሔር እይታ ወይም የእግዚአብሔርን ግምገማ የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ አንተን ገምግሜ ዕውቅና ሰጥቼሃለሁ ወይም በአንተ ተደስቻለሁ/በአንተ ደስ ይለኛል/

• በስምህም ስላወቅሁህ (ዘይቤያዊ ንግግር)

አንድን ሰው በስም ማወቅ ያንን ሰው በሚገባ ወይም በትክክል እንደማወቅ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ አንተን በደንብ ወይም በሚገባ አውቅሃለሁ

Exodus 33:19

• እኔ መልካምነቴን ሁሉ በፊትህ አሳልፋለሁ

እግዚአብሔር (ያህዌ) ከሙሴ ፊት መልካምንቱን አሳልፎ የእግዚአብሔር መልካምነት በፊቱ እንደሚሄድ ዓይነት አቀራረብ አለው። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ የእኔን መልካምነት እንዲታይ መልካምነቴን በፊት አሳልፋለሁ

Exodus 33:21

• እነሆ

“እይ” ወይም “ስማ” ወይም “አድምጠኝ” እንደማለት ነው። ቃሉ በዕብራይስጥ ትኩረት ለመሳብ ወይም የሀሳብ አንድነት መኖሩን ለማመልከት የገባ ነው።

• ጀርባዬንም ታያለህ

እግዚአብሔር ከሙሴ ፊት ለፊት ስለሚሄድ ሙሴ ማየት የሚችለው የእግዚአብሔርን (ያህዌ) ጀርባ ነው

• ፊቴ ግን አይታይም

እግዚአብሔር በሙሴ ፊት ስለሚሄድ ጀርባውን እንጂ ፊቱን ማየት አይሆንለትም። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ ፊቴን ማየት አትችልም


Chapter 34

1 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ “ሁለት የድንጋይ ጽላትን እንደ መጀመሪያዎቹ ጽላት አድርገህ ጥረብ። በሰበርሃቸው በመጀመሪያዎቹ ጽላት ላይ ተጽፈው የነበሩ ቃሎችን በእነዚህ ጽላት ላይ እጽፍባቸዋለሁ። 2 ማለዳ ላይ ተዘጋጅተህ ወደ ሲና ተራራ ውጣና በዚያ በተራራው ዐናት ላይ በፊቴ ቁም። 3 ከአንተ ጋር ማንም ሰው አይምጣ። በተራራው ላይ በየትኛውም ስፍራ ማንም እንዲታይ አታድርግ። የበግና የፍየል መንጋዎች፣ የቀንድ ከብቶችም እንኳ በተራራው ፊት ለፊት ሣር መጋጥ የለባቸውም።” 4 ሁለት የድንጋይ ጽላትን እንድ መጀመሪያዎቹ አድርጎ ጠረበ፤ እግዚአብሔር እንዳዘዘውም በማለዳ ተነሥቶ ወደ ሲና ተራራ ወጣ። ሙሴ ሁለቱን የድንጋይ ጽላት በእጁ ይዞ ነበር። 5 እግዚአብሔር በደመና ወርዶ ከሙሴ ጋር በእዚያ ቆመ፤ ስሙን እግዚአብሔርንም ዐወጀ። 6 በሙሴ ፊትም እንዲህ እያለ በማወጅ ዐለፈ፤ “እግዚአብሔር፣ ርኅሩኅም ቸርም አምላክ እግዚአብሔር፣ ለቊጣ የዘገየ፣ በጽኑዕ ፍቅርና በታማኝነት ባለ ጸጋ፣ 7 ጽኑዕ ፍቅሩን ለሺሕ ትውልድ የሚጠብቅ፣ ክፋትን፣ ዐመፅንና ኀጢአትን ይቅር የሚል፤ በደለኛውን ግን ከቶ ንጹሕ አያደርገውም። ለአባቶች ኀጢአት ልጆቻቸውንና የልጅ ልጆቻቸውን እስከ ሦስትና እስከ አራት ትውልድ ድረስ ይቀጣል።” 8 ሙሴ ወዲያውኑ ወደ መሬት ዝቅ ብሎ ሰገደ። 9 አለ፤ “ጌታዬ ሆይ በፊትህ ሞገስ አግኝቼ ከሆነ፣ እባክህ ዐብረኸን ሂድ፤ ይህ ሕዝብ ግትር ሕዝብ ቢሆንም፣ ክፋታችንና ኀጢአታችንን ይቅር በለን፤ ርስትህም አድርገህ ውሰደን።” 10 እንዲህ አለ፤ “እነሆ፣ ኪዳን እገባለሁ። በምድር ሁሉ አየትኛውም ሕዝብ ዘንድ ተደርገው የማያውቁ ድንቆችን በሕዝብህ ሁሉ ፊት አደርጋለሁ። በአንተ ዘንድ የማደርገው የሚያስፈራ ነውና፣ ዐብሮህ ያለው ሕዝብ ሁሉ ሥራዬን ያያል። 11 የማዝዝህን ፈጽም። አሞራውያንን፣ ከነዓናውያንን፣ ኬጤያውያንን፣ ፌርዛውያንን፣ ኢዊያውያንንና ኢያቡሳውያንን በፊትህ አስወጣቸዋለሁ። 12 አገር ኗሪዎች ጋር ኪዳን እንዳታደርግ ተጠንቀቅ፤ አለዚያ በመካከልህ ወጥመድ ይሆኑብሃል። 13 ሰባብሩ፤ የማምለኪያ ዐምዶቻቸውን አድቅቋቸው፤ የአሼራ ዐፀዶቻቸውንም ቍረጡ። 14 ስሜ ‘ቀናተኛ’ የሆነ እኔ እግዚአብሔር ቀናተኛ አምላክ ነኝና ሌላ አምላክ አታምልክ። 15 ስለዚህም ከምድሪቱ ኗሪዎች ጋር ኪዳን እንዳታደርግ ተጠንቀቅ፤ ምክንያቱም አማልክታቸውን በመከተልያመነዝራሉና፣ መሥዋዕትም ያቀርቡላቸዋልና አንተንም አንዱ ስለሚጋብዝህና ከመሥዋዕቱም ጥቂት ስለምትበላ፣ 16 ከዚያም ከሴቶች ልጆቹ የተወሰኑትን ለወንዶች ልጆችህ ትወስዳለህ፤ ሴት ልጆቹም አማልክታቸውን በመከተል ያመነዝራሉ፤ ወንዶች ልጆችህንም ለአማልክታቸው እንዲያመነዝሩ ያደርጓቸዋል። 17 የተሠሩ አማልክትን ለራስህ አታብጅ። 18 የቂጣ በዓልን አክብር። ባዘዝሁህ መሠረት እርሾ ያልገባበትን ዳቦ በተወሰነው ጊዜ በአቢብ ወር ሰባት ቀን ብላ፤ ከግብፅ የወጣሃው በአቢብ ወር ነበርና። 19 በኵር ሁሉ፣ የከብትህም እንኳ ተባዕት በኵር በሙሉ፣ የበሬዎችህም የበጎችም በኵር የእኔ ነው። 20 የአህያውን በኵር በጠቦት ዋጀው፤ ካልዋጀኸው ግን ዐንገቱን ስበረው። በኵር ወንድ ልጆችህን ሁሉ ዋጃቸው። ባዶ እጁን በፊቴ የሚቀርብ ማንም እይኑር። 21 ቀን ሥራ፤ በሰባተኛው ቀን ግን ዕረፍ። በዕርሻና በመከር ጊዜም እንኳ ዕረፍ። 22 ሱባዔ በዓል ከስንዴው በኵራት ጋር፣ የመክተቻውንም በዓል በዓመቱ መጨረሻ አክብር። 23 በአንተ ዘንድ ያለ ወንድ ሁሉ በዓመት ሦስት ጊዜ በእኔ በእስራኤል አምላክ ፊት ይቅረብ። 24 በፊትህ አስወጣቸዋለሁ፤ ወሰንህንም አሰፋዋለሁ። በዓመት ሦስት ጊዜ በእኔ በአምላክህ በእግዚአብሔር ፊት ለመቅረብ ስትወጣ፣ ምድርህን ለመውረርና ለመቆጣጠር ማንም አይመኝም። 25 ደም ከእርሾ ጋር አታቅርብ፤ ወይም በፋሲካ በዓል የቀረበው መሥዋዕት ሥጋ እስከ ማለዳ ተርፎ አይቆይ። 26 የዕርሻህ ምርጥ በኵራት ወደ ቤቴ አምጣ። የፍየልን ግልገል በእናቱ ወተት አትቀቅል።” 27 እግዚአብሔር ሙሴን፣ “እነዚህን ቃሎች ጻፋቸው፤ በተናገርሏቸው በእነዚህ ቃሎች ክአንተና ከእስራኤል ጋር ኪዳን አድርጌአለሁና አለው። 28 አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከእግዚአብሔር ጋር እዚያው ነበረ። ምግብም አልበላም፤ ውሃም አልጠጣም። 29 ሁለቱን የምስክሩን ጽላት በእጁ ይዞ ከሲና ተራራ ወረደ። ከእግዚአብሔር ጋር እየተነጋገረ ሳለ፣ ፊቱ የሚያበራ ምሆኑን አላወቀም። 30 እስራኤላውያን ሙሴን ሲያዩት፣ ፊቱ ይበራ ነበር፤ ስለዚህም ወደ እርሱ ለመጠጋት ፈሩ። 31 ግን ጠራቸው፤ አሮንና የሕዝቡ መሪዎችም ወደ እርሱ መቱ፣ ሙሴም ከእነርሱ ጋር ተነጋገረ። 32 ከዚያ በኋላም፣ የእስራኤል ሰዎች ሁሉ ወደ ሙሴ መጡ፤ እርሱም በሲና ተራራ ላይ እግዚአብሔር ሰጥቶት የነበረውን ትእዛዝ ሁሉ ነገራቸው። 33 ንግግሩን ከጨረሰ በኋላ፣ በፊቱ ላይ መሸፈኛ አደረገ። 34 ከእግዚአብሔር ጋር ለመነጋገር በፊቱ በሚቀርብበት ጊዜ ሁሉ፣ እስከሚወጣበት ጊዜ ድረስ መሸፈኛውን ያወልቀው ነበር። ሲወጣ ምን እንዲል እንደታዘዘ ለእስራኤላይዋን ይነግራቸዋል። 35 እስራኤላውያን የሚያበራውን ፊቱን ሲያዩ፣ ከእግዚአብሔር ጋር ለመነጋገር ተመልሶ እስኪሄድ ድረስ መሸፈኛውን እንደ ገና በፊቱ ላይ ያደርገዋል።



Exodus 34:1

• የድንጋይ ጽላቶች

ጠፍጣፋ ድንጋዮች (ዘጸአት 31፡18 ተመልከት)

Exodus 34:3

• ከአንተም ጋር ማንም ሰው አይውጣ፥ በተራራውም ሁሉ ማንም አይታይ

በተራራው ላይ መታየት በተራራው ላይ አንድ ሥራ እንደ መሥራት ይቆጠራል። አማራጭ ትርጉም፦ ከአንተ ጋር ማንም ሰው አይምጣ፤ በተራራው በማንኛውም በኩል ወይም ቦታ ማንም ሰው አይታይ

• መንጎችና ከብቶችም በዚያ ተራራ ፊት አይሰማሩ

በግ ወይም ከብት ማንኛውም እንስሳ በተራራው ግርጌ ወይም አጠገብ አይሰማራ

Exodus 34:5

• በዚያም ከእርሱ ጋር ቆመ

“እግዚአብሔር በተራራው ላይ ከሙሴ ጋር ቆመ”

• የእግዚአብሔርንም ስም አወጀ

የዚህ ዐረፍተ ነገር ፍቺ 1) እርሱ ስሙን እግዚአብሔር (ያህዌ) ብሎ ተናገረ 2) እርሱ እግዚአብሔር (ያህዌ) ማን እንደሆነ ተናገረ። ስሙ እግዚአብሔር ማን እንደሆነ አመልካች ነውና።

• እግዚአብሔር፥ እግዚአብሔር መሐሪ፥ ሞገስ ያለው

እግዚአብሔር ስለራሱ ይናገራል፤ አማራጭ ትርጉም፦ እኔ እግዚአብሔር (ያህዌ) ርህሩህና መሐሪ አምላክ ነኝ

• ታጋሽም፥ ባለ ብዙ ቸርነትና እውነት

ይህ አባባል በተለያዩ ቅጂዎች በሁለት መንገድ ይታያል። አንዳንድ ቅጂዎች በአንደኛ መደብ ሲንገሩ ሌሎች በ3ኛ መደብ ይናገራል። ስለዚህ በሁለቱም ትክክል ናቸው፤ 1) እኔ ለቊጣ የዘገየሁ፤ ዘለዓለማዊ ፍቅሬና ታማኝነቴ የበዛ ነው 2) እግዚአብሔር (ያህዌ) ለቍጣ የዘገየ፣ ፍቅሩና ታማኝነቱ የበዛ ነው

• እስከ ሺህ ትውልድም ቸርነትን የሚጠብቅ

ቃል ኪዳኔን እስከ ሽህ ትውልድ ድረስ እጠብቃለሁ ወይም ዘለዓለማዊ ፍቅሬንም እስከ ብዙ ሺህ ትውልድ እጠብቃለሁ

• በደለኛውን ግን ሳይቀጣ ዝም ብሎ አይተውም

በሶስተኛ መደብ የተነገረው እግዚአብሔር ራሱን በሶስተኛ መደብ ሲናገር ይታያል። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ እግዚአብሔር ሀጢአተኛውን/በደለኛውን ሳልቀጣ አልተውም

• በአባቶች ኀጢአት ልጆችን የልጅ ልጆቻቸውን እስከ ሦስትና አራት ትውልድ ይቀጣል

በአባቶች ሀጢአት ምክንያት ልጆቻችሁንና ልጅ ልጆቻችሁን እስከ ሶስትና አራት ትውልድ ድረስ እቀጣለሁ

Exodus 34:8

• በፊትህ ሞገስ አግኝቼ ከሆነ

በዚህ ሀረግ “ሞገስ አግኝቼ” የሚለው የሚያመለክተው ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን ዕውቅና ያገኘ ወይም እግዚአብሔር (ያህዌ) በሙሴ ደስ ተሰኘ ማለት ነው። “በፊትህ” የተባለው በእግዚአብሔር እይታ ወይም የእግዚአብሔርን ግምገማ የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ አንተን ገምግሜ ዕውቅና ሰጥቼሃለሁ፤ ወይም በአንተ ተደስቻለሁ/በአንተ ደስ ይለኛል/

• ክፋታችንንና ኀጢአታችንን ይቅር በል

ሁለቱ ቃላት የፍች ተመሳሳይነት ቢኖራቸውም ልዩነት በመካከላቸው እንዳለ እሙን ነው። እዚህ ጋር በአንድ ላይ የመጡበት ምክንያት አጽንኦት ለመስጠት ነው። ሁለቱን ቃላት ለየብቻ ለመተርጎም የማይቻል ከሆነ ሀጢአታችንን ሁሉ ይቅር በለን ማለት ይቻላል።

• እንደ ርስትህም አድርገህ ውሰደን

ይህ አነጋገር አንድ ሰው አንድን ንብረት ካለበት ቦታ እንደሚወስድ ዓይነት አነጋገር ርስትህ አድርገህ ውሰደን ይላል። አማራጭ ትርጉም፦ የራስህ ሕዝብ አድርገህ ተቀበለን ወይም እኛን ህዝብህን እንደ ርስትህ የራስህ አድርገህ ተቀበለን

Exodus 34:10

• በሕዝብህ ሁሉ ፊት ድንቅ አደርጋለሁ

“በህዝብህ” የተባለው አንተ በምትመራው ህዝብ ፊት ወይም አንተ የምትመራው ህዝብ ሁሉ እያየ

• እኔም በአንተ ዘንድ የምሠራው ነገር የሚያስፈራ ነውና (ዘይቤያዊ ንግግር)

ይህ የሚያስፈራው ነገር ህዝቡ እንዲፈራ የሚያደርግ ነገር ይሆናል። በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር የሚያደርገውን ነገር አይቶ ህዝቡ ይፈራል ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ ለአንተ የማደርገው ነገር ህዝቡ እኔን እንዲፈራ የሚያደርግ ነው

• በአንተ ዘንድ የምሠራው

“በአንተ ዘንድ” የተባለው ሙሴንና የእስራኤልን ህዝብ የሚመለከት ነው

Exodus 34:12

አጠቃልይ ዕይታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴና እስራኤላውያን ማድረግ ያለባቸውን ነገር እየቀጠለ ይናገራል።

• በመካከልህ ወጥመድ እንዳይሆኑብህ

ሌሎችን ሀጢአት እንዲሰሩ የሚያደርጉ እንደ ወጥመድ ተቆጥረዋል። አማራጭ ትርጉም፦ እነርሱ ሀጢአት እንድትሰሩ ያደርጓችኋል

• ስሙ ቀናተኛ የሆነ እግዚአብሔር (ምትካዊ ዘይቤ)

“ቀናተኛ” የተባለው እግዚአብሔር ክብሩን ለማንም እንደማያጋራና የራሱን ክብር እንደሚጠብቅ የሚያሳይ ነው። የእግዚአብሔር ህዝብ ሌሎች አማልክት ቢያመልኩ እግዚአብሔር ክብሩ ይነካል፤ ምክንያቱም የእርሱ የሆኑት እርሱን የማያመልኩ ከሆነ ሌሎችም አያመልኩትም ማለት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ እግዚአብሔር ሁልጊዜ ክብሬን እጠብቃለሁ

• ቅንዓት ያለው አምላክ ነውና

ይህ የእግዚአብሔርን ባህርይ የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እኔ እግዚአብሔር ቀናተኛ አምላክ ስለ ሆንኩ

Exodus 34:15

ቀጥሎ እግዚአብሔር የሚናገረው እስራኤላውያን ከሌሎች ህዝቦች ጋር ያላቸው ግንኙነት ምን መምሰል እንዳለበት ያሳያቸዋል።

ቀጥሎ እግዚአብሔር የሚናገረው እስራኤላውያን ከሌሎች ህዝቦች ጋር ያላቸው ግንኙነት ምን መምሰል እንዳለበት ያሳያቸዋል።

• ባመነዘሩና በሠዉላቸው ጊዜ እንዳይጠሩህ

እግዚአብሔር (ያህዌ) ሌሎች አማልክትን ማምለክ ከሌላ ወንድ ጋር እንደማመንዘር እንደሆነ ይነግራቸዋል። አማራጭ ትርጉም፦ “እነርሱ ሌሎች አማልክት አመለኩ” ወይም “ምክንያቱም እነርሱ ወደ ሌላ ወንድ እንደሚሄዱ አመንዝራዎች ሌሎች አማልክትን አምልከዋል”

• ከመሥዋዕታቸውም እንዳትበላ

ለሌሎች አማልክት የተሰዋን ምግብ መብላት ምን ያህል ክፉ እንደሆነ በግልጽ ያትታል። አማራጭ ትርጉም፦ አንተ (እናንተ) እነርሱ ለአማልክታቸው የሚያቀርቡትን (የሚሰውትን) ምግብ በመብላት አማልክቶቻቸውን ለማምለክ ትፈተናላችሁ ወይም እነርሱ ለአማልክቶቻቸው የሰውትን ምግብ በመብላት ራሳችሁን አመንዝራ ታደርጋላችሁ

Exodus 34:18

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው በሙሴ በኩል ያሳስባቸዋል።

• ሰባት ቀን

ለሰባት ቀን ወይም እስከ ሰባት ቀን

• በአቢብ ወር ከግብፅ ወጥተሃልና

እስራኤላውያን ከግብጽ የወጡት በአቢብ ወር ስለሆነ ለእነርሱ የአመቱ መጀመሪያ ወር ነው። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር አቢብ ወር የሚጀምረው ከመጋቢት መጨረሻ ሳምንት እስከ ሚያዝያ መጀመሪያ ሳምንት ድረስ ነው። (ዘጸአት 13፡4 ተመልከት)።

Exodus 34:19

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው በሙሴ በኩል ያሳስባቸዋል።

• ማኅፀንንም የሚከፍት (ዘይቤያዊ አነጋገር)

በኩር ሆኖ የሚወለድ ወይም የሚወጣ

• ትዋጀዋለህ

በኩር ሆኖ የሚወለድ ወንድ እና አህያ የእግዚአብሔር (የያህዌ) ነው፤ ነገር ግን መስዋእት ሆነው እንዲቀርቡለት ያህዌ አይፈልግም። በእነርሱ ፋንታ እስራኤላውያን በጎችን እንዲሰዉለት ተጠይቀዋል። ስለሆነም እስራኤላውያን በኩር ሆኖ የተወለደን አህያ ወይም ወንድ ልጅ ከእግዚአብሔር መልሰው እንዲገዙ ተፈቅዶላቸዋል። የምይዋጁ ከሆነ አንገቱን ቆልምመው ለመስዋዕት እንዳይቀርብ እንድያደርጉ ተጠይቀዋል።

• በፊቴም አንድ ሰው ባዶ እጁን አይታይ

ይህ አነጋገር እግዚአብሔር ማንም ሰው ወደ ፊቱ ሲመጣ የሆነ ነገር ተሸክሞ እንድመጣ የሚጠይቅ ይመስላል። ነገር ግን ይህ ወካይ ዘይቤ የሚያሳየው ወደ እኔ የሚመጣ ማንም ቢሆን መስዋዕት ሳይዝ አይምጣ ወይም ወደ እኔ የሚመጣ ማንም ቢሆን መስዋዕት ማምጣት አለበት

Exodus 34:21

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው በሙሴ በኩል ያሳስባቸዋል።

• በምታርስበትና በምታጭድበት ዘመን ታርፋለህ

“በእርሻም ወቅትም ሆነ በመከር ወቅት በሰባተኛው ቀን ምንም ሥራ አትሥሩ” ወይም “በእርሻና በመከር ጊዜ እንኳ ቢሆን ማረፍ አለብህ”

• የመክተቻ በዓል

ይህ በዓል የዳስ በመባል ይታወቃል። ይህ ልምምድ የመጣው እርሻቸውን በዳስ ወይም በጊዜያዊ ጎጆ ውስጥ ሆነው ያረሱና እህሉ እስኪደርስ ድረስ በዚያ ዳስ ሆነው ከአውሬ ሲጠብቁ የነበሩ አርሶ አደሮች ልምምድ ነው። “መክተቻ” የተባለው የእህል ማከማቻ ማለት ነው።

Exodus 34:23

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው በሙሴ በኩል ያሳስባቸዋል

Exodus 34:25

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤላውያን ምን ማድረግ እንዳለባቸው በሙሴ በኩል ያሳስባቸዋል

• የመሥዋዕቴን ደም

ደሙ መስዋዕት ከሚቀርበው እንስሳ የተገኘ ሲሆን የተሰዋው ለእግዚአብሔር ነበር። አማራጭ ትርጉም፦ የእንስሳ ደም ለእኔ በምታቀርብበት ጊዜ

• ከቦካ እንጀራ ጋር

እርሾ ካለው ወይም ከገባበት ከማንኛውም ነገር ጋር

Exodus 34:27

• በዚያም አርባ ቀንና አርባ ሌሊት

በተራራው ላይ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት

• በጽላቶቹም አሥሩን የቃል ኪዳን ቃሎች ጻፈ

በጽላቶቹ ላይ የቃል ኪዳን ቃላት የሆኑትን ዐሥሩን ትእዛዞች የጻፈው ሙሴ ይሁን ወይስ እግዚአብሔር ግልጽ አይደለም። እንደዚህኛው አባባል የጻፈው ሙሴ እንደሆነ ያሳይል ነገር ግን ከሌሎች አውድ ስንመለከት የጻፈው እግዚአብሔር (ያህዌ) ነው። “እርሱ” የሚለው ተውላጠ ስም ስለማን እንደሆነ አጠያያቂ ነው

Exodus 34:29

• የፊቱ ቁርበት እንዳንጸባረቀ

በሌላ አገላለጽ፦ “የግንባሩ ቆዳ” ማለት ሲሆን ጠቅላላ “ፊቱን” የሚመለከት ነው። ፊቱ እንደሚያበራ ወይም እንደሚያንጸባርቅ ሆነ ወይም ፊቱ አበራ ወይም አንጻባረቀ

• ወደ እርሱም ይቀርቡ ዘንድ ፈሩ

ወደ ሙሴ ለመቅረብ ፈሩ ወይም ፈርተው ነበር

• ወደ እርሱ ተመለሱ

ወደ ሙሴ ተመልሰው መጡ

Exodus 34:32

• እግዚአብሔርም በሲና ተራራ የተናገረውን ነገር ሁሉ አዘዛቸው

ሙሴም እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ የገለጠለትን ሕግ ሁሉ ለእስራኤላውያን ሰጣቸው ወይም እንዲያደርጉ አዘዛቸው

Exodus 34:34

• መሸፈኛውን ከፊቱ አነሣ

መሸፈኛውን ወይም ሻሹን ከፊቱ ላይ ያነሳ ነበር

• የታዘዘውን ነገር ነገረ

እግዚአብሔር (ያህዌ) እርሱን (ሙሴን) ያዘዘውን ነገር እርሱ ለእስራኤላውያን ነገራቸው ማለት ነው


Chapter 35

1 የእስራኤልን ማኅበረ ሰብ ሁሉ ሰብስቦ እንዲህ አላቸው፤ “እንድትፈጽሟቸው እግዚአብሔር የሰጣችሁ ትእዛዝት እነዚህ ናቸው። 2 ስድስት ቀን ሥራ ትሠራላችሁ፤ ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር የተቀደሰ የፍጹም ዕረፍት የሰንበት ቀን ይሁንላችሁ። በዚያ ቀን ሥራ የሚሥዐራ ሁሉ ይሞታል። 3 በሰንበት ቀን በማንኛችሁም ቤት ውስጥ እሳት አይንደድ።” 4 ሁሉን የእስራኤል ማኅበረ ሰብ እንዲህ አላቸው፤ “እግዚአብሔር ያዘዘው ይህ ነው። 5 ከልብ ፈቃደኛ የሆናችሁ ሁሉ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አቅርቡ። ሁሉም ለእግዚአብሔር የወርቅ፣ የብር፣ የነሐስ መባያምጣ፤ 6 ሐምራዊና ቀይ ማግ፣ ቀጭን በፍታ፣ የፍየል ጠጒር፣ 7 በቀይ ቀለም የተነከረ የአውራ በግ ቆዳና የአቆስጣ ቆዳ፣ የግራር ዕንጨት፣ 8 መብራቶች ዘይት፣ ለመቅቢያ ዘይቱ ቅመምና ጣፋጭ መዐዛ ያለው ዕጣን፣ 9 መረግዶችና ለኤፉዱና ለደረት ኪሱ የሚሆኑ ሌሎች ዕንጨቶችንም መባ አድርጎ ያቅርብ። 10 በመካከላችሁ ያሉ ብልኀተኛ ሰዎች ሁሉ ይምጡና እግዚአብሔር ያዘዘውን ሁሉ ይሥሩ፦ 11 ከድንኳኑ ጋር፣ መደሪያውን፣ ማያያዣዎቹን፣ ክፈፎቹን፣ አግዳሚዎቹን፣ ቋሚዎቹንና መሠረቶቹን፤ 12 ታቦቱንም ከነመሎጊያዎቹ፣ የስርየት መክደኛውንና የሚሸፍነውን መጋረጃ፤ 13 ከመሎጊያዎቹ ጋር፣ ዕቃዎቹንም ሁሉን ኣየገጽ ኅብስቱን፤ 14 የመብራቶቹን መቅረዝ ከዐባሪ ዕቃዎቹ ጋር፣ መብራቶቹንና የመብራቶቹን ዘይት፤ 15 የዕጣኑን መሠዊያ ከመሎጊያዎቹ ጋር፣ መቅቢያ ዘይቱንና ጣፋጭ መዓዛ ያለውን ዕጣን፣ የመገናኛ ድንኳኑን መግቢያ መጋረጃ፣ 16 የሚቃጠሉ መሥዋዕቶችን መሠዊያ ከነሐስ መጫሪያው፣ ከመሎጊያዎቹና ከዕቃዎቹ ጋር፤ ትልቁን የመታጠቢያ ሰን እስከ ማስቀመጫው፤ 17 የአድደባባዩን መጋረጃዎች ከምሰሶዎቹና ከመሠረቶቹ ጋር፣ የአደባባዩን መግቢይ ኣመጋረጃ፤ 18 የማደሪያውን ድንኳን ካስማዎች ከነገመዶቻቸው፤ 19 ውስጥ ለማገልገል በብልኀት የተሠሩ ልብሶችን፣ ካህናት ሆነው ለማገልገል ለካህኑ ለአሮንና ለልጆቹ የሚሆኑ የተቀደሱ ልብሶችን ያምጡ።” 20 ከዚያም ሁሉም የእስራኤል ነገዶች ሁሉ ከሙሴ ፊት ወጥተው ሄዱ። 21 ልቡ የተነሣሣና ፈቃደኛ የሆነ ሁሉ በመምጣት ለመገናኛው ድንኳን ሥራ፣ ለውስጡም ለሚደረገው አገልግሎትና ለተቀደሱ ልብሶች የሚሆን ስጦታን ሰጡ። 22 ፈቃደኛ የነበሩ ወንዶችም ሴቶችም መጥተው የአፍንጫ ጌጦችን፣ የጆሮ ጌጦችን፣ ቀለበቶችን፣ ድሪዎችንና ሁሉንም ዓይነት የወርቅ ጌጣጌጦች አመጡ። 23 ሐምራዊ፣ ቀይም ቀይ ማግ፣ ያማረ በፍታ፣ የፍየል ጠጕር፣ በቀይ ቀለም የተነከረ የአውራ በግ ቆዳ፣ ወይም የአስቆጣ ቆዳ የነበራቸውም አመጡ። 24 ለማንኛውም ተግባር የሚጠቅም የግራር ዕንጨት የነራቸው፣ የብርና የነሐስ ስጦታ ማድረግ የሚፈልጉ ሁሉ በስጦታነት ለእግዚአብሔር አቀረቡ። 25 ብልኀተኛ ሴቶችም ሁሉ ማግ ፈትለው፣ የፈተሉትን ሰማያዊ፣ ሕዐምራዊ፣ ወይም ቀይ ማግ አመጡ። 26 ያነሣሣቸውና ብልኀተኛ የሆኑ ሴቶች ሁሉ የፍየል ጠጕር ፈተሉ። 27 ለአፉዱና ለደረት ኪሱ የሚሆኑ መረግዶችንና ሌሎች ዕንቆችን አመጡ፤ 28 ለመቅቢያው ዘይትና ጣፋጭ መዐዛ ላለው ዕጣን ዘይትና ቅመምም አመጡ። 29 የነጻ ፈቃድ ስጦታ ለእግዚአብሔር በሙሴ በኩል እንዲፈጸም አዝዞት ለነበረው ሥራ ሁሉ ቍሳቍሶችን አመጡ። 30 እስራኤላውያንን እንዲህ አላቸው፤ “እነሆ፣ እግዚአብሔር የሖር የልጅ ልጅ የሆነውን የኡሪን ልጅ ባስልኤልን ከይሁዳ ነገድ በስም ጠርቶታል። 31 ለሁሉም ዐይነት የጥበብ ሥራ ጥበብን፣ ማስተዋልንና ዕውቀትን ሊሰጠው ባስልኤልን በመንፈሱ ሞልቶታል፤ 32 የወርቅ፣ የብርና የነሐስ ጥበባዊ ሥራዎችን ለመሥራት፣ 33 የጥበባዊ ሥራ ዐይነቶችን ሁሉ ለመሥራት ድንጋዮችን እንዲጠርብና ዕንጨትም እንዲቀርጽ ነው። 34 እግዚአብሔር በባስልኤልና ከዳን ነገድ በሆነው በአሂሳሚክ ልጅ በኤልያብ ልብ ይህን ችሎታ አስቀመጠ። 35 ጥበበኛ ሰዎች፣ እንደ ቀራጺዎች፣ በሰማያዊ፣ በሐምራዊና በቀይ ማግ፣ ባማረ በፍታም እንደ ጥልፍ ጠላፊዎችና እንደ ሸመና ሠራተኞች እንዲሠሩም ብልኀትን ሞላባቸው። እነርሱ በሥራ ዐይነቶች ሁሉ ጥበበኞች የሆኑ የጥበብ ባለሙያዎች ናቸው።



Exodus 35:1

• ሰባተኛው ቀን

የሳምንቱ ሰባተኛ ቀን ወይም በአይሁዶች አቆጣጠር ቅዳሜ ማለት ነው

• የሚሰራበትም ሁሉ ይገደል

ይህ በተደራጊ ግስ የተጻፈው በአድራጊ ግስ ሲጻፍ፦ በዚህ ቀን ሥራ የሚሠራበት ማንኛውም ሰው ግደሉት

Exodus 35:4

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን ያዘዛቸው ነገሮች እርሱ እስራኤላውያን እንዲያደርጉ ይነግራቸዋል።

• ለእግዚአብሔር ቁርባንን አቅርቡ

ለእግዚአብሔር መባ ወይም መስዋዕት አቅርቡ

• የልብ ፈቃድ ያለው

“ልብ” መባውን የሚያቀርበውን ሰው ማመልከቱ ነው። አማራጭ ትርጉም፦ እያንዳንዱ ሰው ልቡ የፈቀደውን ወይም ፈቃደኛ የሆነ ማንም ሰው”

Exodus 35:10

አጠቃላይ ምልከታ፦

እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን ያዘዛቸው ነገሮች እርሱ እስራኤላውያን እንዲያደርጉ ቀጥሎ ይነግራቸዋል።

• በልባቸው ጥበበኞች ሁሉ

የእጅ ጥበብ ዐዋቂዎች ሁሉ ወይም ጥበብ ያለው እያንዳንዱ ሰው

• መያዣዎቹንም

መጋረጃዎችን ለማገናኘት የሚያገለግሉ ቀለበቶች ናቸው (ዘጸአት 26፡4-6 ተመልከት)

• እግሮቹንም

በመሬት ላይ የተሰኩና ሌሎችን ከመሬት ጋር ለማገናኘትና እንዳይንቀሳቀሱ ለማድረግ የሚያገልግሉ እንደመሰረት የሚያገለግሉ ናቸው (ዘጸአት 26፡31)

• የስርየት መክደኛውንም

በታቦቱ ላይ የሚቀመጠው የማስተሰሪያ መስዋዕት የተሰራበት መክደኛ ወይም መሸፈኛ

Exodus 35:13

• የገጹንም ኅብስት

ይህ ዳቦ ወይም ህብስት የእግዚአብሔርን ህልዎት የሚወክል ነው። (ዘጸአት 25፡30 ተመልከት)

• የናሱንም መከታ

እንጨት ሲቃጠል ለመያዣነት የሚያገለግል የነሐስ መከላከያ ብረት

Exodus 35:17

• ምሰሶቹንም

ቀጥ ብለው የቆሙና ድጋፍ የሚሰጡ እንጨቶች ናቸው።

• እግሮቻቸውንም

በመሬት ላይ የተሰኩና ሌሎችን ከመሬት ጋር ለማገናኘትና እንዳይንቀሳቀሱ ለማድረግ የሚያገልግሉ እንደመሰረት የሚያገለግሉ ናቸው (ዘጸአት 26፡19)

• ካስማዎች

ከእንጨት ወይም ከብረት የተሰሩ የድንኳን ጠርዞችን ወይም ማዕዘኖችን ለመወጠር የሚያገለግሉ ናቸው (ዘጸአት 27፡19 ተመልከት)

• በብልሃት የተሠሩትን ልብሶች

በጥበብ ያጌጡ ወይም የተቀደሱ ልብሶች

Exodus 35:20

• የእስራኤልም ልጆች ማኅበር ሁሉ

እያንዳንዱን ነገር የሚመለከት ነው። ከእያንዳንዱ ነገድ የሆኑ የእስራኤል ህዝቦች

• ሰው ሁሉ ልቡ እንዳነሣሣው

“ልብ” የሰውየው ማንነት የሚመለከት ሲሆን ልቡ ለእግዚአብሔር ነገር ክፍት የሆነ ለመስጠት ልቡ የፈቀደው ወይም ያነሳሳው

• መንፈሱም እሺ እንዳሰኘው

“መንፈስ” የሰው ማንነት መግለጫ ሲሆን የሰው መንፈስ ወይም ፈቃድ አመልካች ነው። መንፈሱ የፈቀደው ወይም ፈቃደኛ የሆነ ማለት ነው።

• ልባቸው እንደ ፈቀደ

ፈቃደኛ የነበሩ ወይም የሆኑ

Exodus 35:23

ለቁጥር 23 ዘጸአት 25፡4-5 ትርጉም ተመልከት

ለቁጥር 23 ዘጸአት 25፡4-5 ትርጉም ተመልከት

Exodus 35:25

• የፈተሉትንም ሰማያዊውን ሐምራዊውንም ቀዩንም ግምጃ

በእጃቸው የሠሩትን ጥሩ በፍታ ወይም ማግ በሰማያዊ፥ በሐምራዊና በቀይ ቀለም ቀለሙት

• ልባቸውም በጥበብ ያስነሣቸው

“ልብ” ሴቶችን የሚመለከት ሲሆን ፈቃደኛ የነበሩና ጥበብ ያላቸው ሴቶች ማለት ነው

Exodus 35:27

አለቆችም . . . ሙሴ ይሠራ ዘንድ እግዚአብሔር ላዘዘው ሥራ . . . አመጡ

ከቁጥር 27-29 ያለውን ክፍል ከምዕራፍ 25፡1-2 እና ቁጥር 3-7 በማነጻጸር ተርጉም።

Exodus 35:30

• የእግዚአብሔርን መንፈስ ሞላበት

የመንፈስ መሞላት አንድ ባዶ ነገር ውስጥ እንድን ነገር እንደመሙላት ይቆጠራል። የእግዚአብሔር መንፈስ ችሎታ ሰጠው።

• በሥራ ሁሉ ብልሃት

ማናቸውንም የጥበብ ሥራ መሥራት እንዲችል (ዘጸአት 31፡1-2 እና 31፡3-5)

Exodus 35:34

አጠቃላይ ምልከታ፦

ሙሴ ለህዝቡ ንግግሩን ይቀጥላል

• ያስተምሩ ዘንድ በልባቸው አሳደረባቸው

“በልባቸው” የሚለው ባስልኤልና የእርሱን የሥራ ጓደኞችን የሚመለከት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ ዕውቀታቸውን ለሌሎች የማስተማርን ችሎታ ሰጥቶአቸዋል

• በብልሃት የሚሠራውን ሁሉ ያደርጉ ዘንድ

ማናቸውንም የጥበብ ሥራ ለመሥራት እንዲችሉ

• በእነርሱ ልብ ጥበብን ሞላ

ማንኛውንም ዐይነት ሥራ ያከናውኑ ዘንድ ጥበብን ሰጣቸው


Chapter 36

1 ስለዚህ ባስልኤልና ኤልያብ፣ የልብ ጥበበኞች የነበሩና እንዲፈጽሙት እግዚአብሔር ያዘዘውን በመከተል መቅደሱ እንዴት እንደሚሠራ ለማወቅ ብልኀትንና ማስተዋልን ያስቀመጠባቸውም ሁሉ ይሠራሉ። 2 ባስልኤልንና ኤልያብን፣ እግዚአብሔር በልቡ ብልኀትን አስቀምጦበት የነበረ ጥበበኛ ስውን ሁሉ፣ መጥቶ ሥራውን ለመሥራት ልቡ ያነሣሣውንም ጠራ። 3 የጠራቸውም ለመቅደሱ ሥራ እስራኤላውያን አምጥተውት የነበረውን ስጦታ ሁሉ ከሙሴ ተቀበሉ። ሕዝቡ የነጻ ፈቃድ ስጦታዎችን ጠዋት ጠዋት ወደ ሙሴ ማምጣት አላቋረጡም ነበር። 4 ስለዚህ በመቅደሱ ሥራ ላይ የተሰማሩ ብልኀተኛ ሰዎች ሁሉ ከሚሠሩት ሥራ ተነሥተው መጡ። 5 ሙሴን፣ “እግዚአብሔር እንድንሠራው ላዘዘን ሥራ ከሚበቃው በጣም የሚበልጥ ሕዝቡ እያመጡ ነው” አሉት። 6 ሙሴም በሰፈሩ ውስጥ ያለ ማንም ሰው ለመቅደሱ ሥራ ሌላ ስጦታ እንዳያመጣ ትእዛዝ ሰጠ። ከዚያም በኋላ ሕዝቡ ስጦታ ማምጣቱን አቆሙ። 7 ለሥራው ሁሉ ከሚበቃው በላይ ቍሳቍሶች ነበሯቸው። 8 ያሉ ጥበበኞችም ሁሉ ከአማረ በፍታና ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግም ከተሠሩትና ኪሩቤልም ከተጠለፉባቸው ዕሥር መጋረጃዎች ጋር የመገናኛውን ድንኳን ሠሩት። ይህም እጅግ ጥበበኛ የነበረው የባስልኤል ሥራ ነው። 9 መጋረጃ እርዝመት ሃያ ስምንት ክንድ፣ ወርዱም አራት ክንድ ነበረ። ሁሉም መጋረጃዎች እኩል መጠን ነበራቸው። 10 ባስልኤል ዐምስት ዐምስቱን መጋረጃዎች በአንድ ላይ አድርጎ እርስ በርስ አገጣጠማቸው። 11 መጋረጃዎች የመጨረሻ የውጭ ጠርዝ ላይና በሁለተኛውም ተገጣጣሚ መጋረጃ የመጨረሻ የውጭ ጠርዝ ላይ ሰማያዊ ቀለበቶችን አደረገ። 12 በሁለተኛው መጋረጃ ጠርዞች ዐምሳ ዐምሳ ቀለበቶችን አበጀ። ስለሆነም ቀለበቶቹ እርስ በርስ ትይዩ ሆነው የተደረጉ ነበር። 13 ባስልኤል ዐምሳ የወርቅ ማያያዣዎችን ሠርቶ የመገናኛው ድንኳን ወጥ እንዲሆን መጋረጃዎቹን አያያዛቸው። 14 ባስልኤል በማደሪያው ላይ ላለው ድንኳን ዐሥራ አንድ የፍየል ጠጕር መጋረጃዎችን ሠራ። 15 የእያንዳንዱ መጋረጃ እርዝመት ሠላሳ ክንድ፣ ወርዱም አራት ክንድ ነበረ። ዐሥራ አንድ መጋረጃዎች እያንዳንዳቸው እኩል መጠን ነበራቸው። 16 መጋረጃዎች እርስ በርሳቸው፣ ስድስቱንም መጋረጃዎች እንደዚሁ እርስ በርሳቸው አያያዛቸው። 17 ተገጣጣሚ መጋረጃዎች የመጨረሻ መጋረጃ ጠርዝ ላይ ዐምሳ ቀለበቶችን በሁለተኛዎቹ ተገጣጣሚ መጋረጃዎች የመጨረሻ መጋረጃ ጠርዝ ላይም እንደዚሁ ዐምሳ ቀለበቶችን አበጀ። 18 ባስልኤል ወጥ እንዲሆን ድንኳኑን ለማገጣጠም ዐምሳ የነሐስ ማያያዣዎችን ሠራ። 19 ለድንኳኑ መሸፈኛ በቀይ ቅለም የተነከረ የአውራ በግ ቆዳ፣ ከበላዩም የሚህን የአቆስጣ ቆዳ ሠራ። 20 ባስልኤል ከግራር ዕንጨት ወጋግራዎችን ለመገናኛው ድንኳን ሠራ። 21 ወጋግራ እርዝመት ዐሥር ክንድ፣ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል ነበር። 22 እርስ በርስ ለማያያዝ በያንዳንዱ ወጋግራ ሁለት ማያያዣዎች ነበር። የመገናኛውን ድንኳን ወጋግራዎች ሁሉ በዚህ መንገድ ሠራ። 23 ባስልኤል በዚህ መንገድ ወጋግራዎችን ለመገናኛው ድንኳን ሠራ። ለደቡቡ ጎንም ሃያ ወጋግራዎችን አበጀ። 24 ባስልኤል ከሃያዎቹ ወጋግራዎች ሥር የሚሆኑ አራ የብር መቆሚያዎችን አበጀ። ማያያዣዎች ለመሆን ከመጀመሪያው ወጋግራ ሥር ሁለት መቆሚያዎች ከያንዳንዱ ሌላ ወጋግራ በታችም እንደዚሁ ሁለት መቆሚያዎች ነበሩ። 25 ጎን ላለው ለመገናኛው ድንኳን ሁለተኛ ጎን ሃያ ወጋግራዎችንና 26 የብር መቆሚያዎቻቸውን አበጀ። በመጀመሪያው ወጋግራ ሥር ሁለት መቆሚያዎች፣ በሚቀጥለው ወጋግራ ሥርም እንዲሁ ሁለት ሁለት መቆሚያ አበጅቶአል። 27 በስተ ምዕራብ ላለው ለመገናኛው ድንኳን ጀርባ ባስልኤል ስድስት ወጋግራዎችን ሠራ። 28 ድንኳን የኋላ ማእዘኖች ሁለት ወጋግራዎችን አበጀ። 29 እነዚህ ወጋግራዎች ከታች የተነጣጠሉ፣ ከላይ ደግሞ በአንድ ቀለበት የየያያዙ ነበር። ለሁለቱም የኋላ ማእዘኖች የተደረገው በዚህ መንገድ ነበር። 30 ከብር መቆሚያዎቻቸው ጋር ስምንት ወጋግራዎች ነበሩ። በመጀመሪያው ወጋግራ ሥር ሁለት መቆሚያዎች፣ በሚቀጥለውም ወጋግራ ሥር ሁለት መቆሚያዎች ለያንዳንዱ ወጋግራ ሁለት ሁለት በመሆን ዐሥራ ስድስት መቆሚያዎች ነበሩ። 31 ባስልኤል የግራር ዕንጨት አግዳሚዎችን አበጀ፦ ለመገናኛው ድንኳን አንድ ጎን ወጋግራዎች ዐምስት፣ አግዳሚዎችን፣ 32 የመገናኛው ድንኳን ጎን ወጋግራዎች አምስት አግዳሚዎችን፣ በምዕራብ በኩል ላለው ለመገናኛው ድንኳን የኋላ ጎን ወጋግራዎችም ዐምስት አግዳሚዎችን ሠራ። 33 አግዳሚዎቹን የሥራቸውም በወጋግራዎች መካከል ላይ ከዳር እስከ ዳር እንዲደርሱ አድርጎ ነው። 34 ወጋግራዎቹን በወርቅ ለበጣቸው። አግዳሚዎችን ለማያያዝ የወርቅ ቀለበቶችን ሠራ፣ አግዳሚዎችንም በወርቅ ለበጣቸው። 35 በብልኀተኛ ሠራተኛ ሥራ ኪሩቤል የተጠለፉበትን መጋረጃ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ፣ ካማረ በፍታም ሠራው። 36 አራት የግራር ዕንጨት ምሰሶዎችን አበጅቶ በውርቅ ለበጣቸው። ለምሰሶዎችም የወርቅ ኵላቦችን ሠርቶ አራት የብር መቆሚያዎችን አደረገላቸው። 37 ለድንኳኑ መግቢያ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ፣ ካማረ በፍታም በጥልፍ ጠላፊ ሥራ የተዘጋጀ መጋረጃ አበጀለት። 38 የመጋረጃውን ዐምስት ምሰሶዎች ከኵላቦች ጋር ሠራ። የምሰሶዎችን ዐናትና ዘንግ በወርቅ ለበጣቸው። ዐምስት መቆሚያዎቻቸውም ከነሐስ የተሰሩ ነበሩ።



Exodus 36:1

• ባስልኤልና ኤልያብ

ሁለቱም ወንዶች ሲሆኑ እግዚአብሔር ለመገናኛው ድንኳን ሥራ የጠራቸው ናቸው (ዘጸአት 31፡1-2፤ 31፡6)

• በልባቸው ጥበበኞችም ሁሉ

እግዚአብሔር ጥበብን በውስጡ እንዳስቀመጠለት የሚለው ዘይቤያዊ አነጋገር ሲሆን እግዚአብሔር ጥበብ የሰጠው ማለት ነው።

• እግዚአብሔር እንዳዘዘው ነገር ሁሉ አደረጉ

እንዲያደርጉ /እንዲሰሩ/ እግዚአብሔር ባዘዘው መንገድ ወይም ልክ እግዚአብሔር እንዳዘዘው

Exodus 36:2

• ባስልኤልና ኤልያብ

ሁለቱም ወንዶች ሲሆኑ እግዚአብሔር ለመገናኛው ድንኳን ሥራ የጠራቸው ናቸው (ዘጸአት 31፡1-2፤ 31፡6)

• እግዚአብሔርም በልቡ ጥበብን ያደረገለትን

እግዚአብሔር ችሎታ የሰጣቸውንና ሥራውን ለመሥራት ፈቃደኛ የሆኑትን ሰዎች ሁሉ

• ልቡ ያስነሣውን ሁሉ

“ልብ” የሰውዬውን ማንነት የሚመለከት ሲሆን ለእግዚአብሔር ሥራ ውስጡ/ልቡ/ፈቃደኛ የሆነ ወይም ለእግዚአብሔር ሥራ ራሱን ያዘጋጀ ወይም ምላሽ የሰጠ ማለት ነው

Exodus 36:5

• የመቅደሱንም ሥራ የሚሠሩ ጠቢባን ሁሉ የሚያደርጉትን ሥራ ትተው መጡ

የመቅደሱን ሥራ የሚሰሩ ጥበበኞች የሆኑ ባለሙያዎች ሥራ ትተው ወደ ሙሴ መጥተው እግዚአብሔር ያዘዘን ሥራ ለመሥራት የሚያስችል በቂና ከበቂ በላይ ስጦታ ህዝቡ እያመጡ ነው ብለው ተናገሩ።

Exodus 36:8

ምዕራፍ 38፡8-10 ካለው ክፍል ጋር አነጻጽር እንዲሁም ምዕራፍ 26፡1-3 ተመልከት።

ምዕራፍ 38፡8-10 ካለው ክፍል ጋር አነጻጽር እንዲሁም ምዕራፍ 26፡1-3 ተመልከት።

• ማደሪያውን ከአሥር መጋረጆች ሠሩ

የማደሪያው ድንኳን መጋረጃዎች በቁጥር አስር ሲሆኑ የተሰሩት ከልብስ ሆኖ አንዱ ከሌላው ጋር በስፌት ተያይዘው በግድግዳው ላይ ይሰቀላሉ።

Exodus 36:11

• የሰማያዊውን ግምጃ ቀለበቶች አደረጉ

ከሰማያዊ ጨርቅ የተሰሩ ቀለበቶች

• መጋረጆች

እነዚህ መጋረጃዎች የመገናኛውን ድንኳን ለመከፋፈልና ለመሸፈን የሚረዱ ሰፊና ከባድ የጨርቅ መጋረጃዎች ናቸው

• አደረጉ

በወል ስም የተጠቀሰው “አደረጉ” የሚለው የሚያመለክተው ባስልኤልና ከእርሱ ጋር የመገናኛውን ድንኳን ሥራ የሚሰሩ ሰዎች ሁሉ የሚዳስስ ነው።

• አምሳ ቀለበቶችንችን

ሀምሳ የወርቅ ቀለበቶችን (ክብ ነገሮችን)

Exodus 36:14

• አሥራ አንድ መጋረጆች አደረጉ

የመጋረጃው ቁጥር 11 መሆኑን ያመለክታል

• ርዝመቱ ሠላሳ ክንድ

ይህ የልከት ዘዴ ባህላዊ ሲሆን የአንድ ሰው ከክንድ መጋጠሚያ እስከ መካከለኛው ጣት ደረስ ያለው ክፍል ነው።

Exodus 36:18

ተመሳሳይ ክፍሎችን ምዕራፍ 26፡11 እና 26፡14 ተመልከት።

ተመሳሳይ ክፍሎችን ምዕራፍ 26፡11 እና 26፡14 ተመልከት።

Exodus 36:20

ምዕራፍ 26፡15-18 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከትና ከዚህኛ ክፍል ትርጉም ጋር አነጻጽር።

ምዕራፍ 26፡15-18 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከትና ከዚህኛ ክፍል ትርጉም ጋር አነጻጽር።

• ለማደሪያውም በደቡብ ወገን ሀያ ሳንቆችን አደረጉ

በደቡብ በኩል ላለው የማደሪያ ድንኳን ሃያ ወጋግራ (ቋሚዎችን) አደረጉ ወም ሰሩ

Exodus 36:24

ከዚህ ክፍል ጋር ተመሳሳይ የሆነውን ዘጸአት 26፡19-21 ተመልከት።

ከዚህ ክፍል ጋር ተመሳሳይ የሆነውን ዘጸአት 26፡19-21 ተመልከት።

• ለሁለተኛው ወገን በሰሜን በኩል ሀያ ሳንቆች

ለሁለተኛው ክፍል በሰሜን በኩል ወጋግራዎች ነበሩ

Exodus 36:27

• በስተ ኋላ ስድስት ሳንቆች አደረጉ

ምዕራፍ 26፡22-23 ያለውን ክፍል እንዴት እንደተረጎምክ እይ

• በምዕራቡ ወገን

በምዕራብ በኩል ባለው

• ለሁለቱ ማዕዘን

ከኋላ በኩል ባለው ለሁለቱ ማዕዘናት

Exodus 36:29

ምዕራፍ 26፡24-25 ተመልከትና ማስተካከያ አድርግ

ምዕራፍ 26፡24-25 ተመልከትና ማስተካከያ አድርግ

Exodus 36:31

ዘጸአት 26፡26-28 እና 26፡29 ተመልከት

ዘጸአት 26፡26-28 እና 26፡29 ተመልከት

• ከዳር እስከ ዳር አሳለፉ

ለመገናኛው ድንኳን ከአንድ ጫፍ ወደ ሌላ ጫፍ መውሰድ ወይም ማሳለፍ

Exodus 36:37

• አምስቱም እግሮቻቸው የናስ ነበሩ

መቆሚያዎች ከነሐስ ብረት የተሰሩ ስለመሆናቸው የሚናገር ነው። ምዕራፍ 26፡36-37 አነጻጽር።


Chapter 37

1 ባስልኤል እርዝመቱ ሁለት ተኩል ክንድ፣ ወርዱ አንድ ተኩል ክንድ፣ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ ታቦታ ከግራር ዕንጨት ሠራ። 2 ውስጡንና ውጩንም በንጹሕ ወርቅ ለበጠው፤ በዙሪያውም የወርቅ ክፈፍ አበጀለት። 3 ለአራት እግሮቹም አራት የወርቅ ቀለበቶችን፣ በአንዱ ጎኑ ላይ ሁለት ቀለበቶችን፣ በሌላውም ጎኑ ላይ ሁለት ቀለበቶችን ጨምሮ ሠራ። 4 ዕንጨት መሎጊያዎችን ሠርቶ በወርቅ ለበጣቸው። 5 ታቦቱን ለመሸከም በታቦቱ ጎኖች ላይ ባሉት ቀለበቶች ውስጥ መሎጊያዎቹን አስገባቸው። 6 ሁለት ተኩል ክንድ፣ ወርዱም አንድ ተኩል ክንድ የሆነ የስርየት መክደኛ ከንጹሕ ወርቅ ሠራ። 7 ባስልኤል ለስርየት መክደኛው ሁለት ጫፎች ሁለት ኪሩቤልን ከተቀጠቀጠ ወርቅ አበጀ። 8 አንዱ ኪሩብ ለአንዱ የስርየት መክደኛ፣ ሌላውም ለሌላው የስርየት መክደኛ ጫፍ ነበረ። ኪሩቤል ከስርየት መክደኛው ጋር ወጥ ሆነው ተበጅተው ነበር። 9 ኪሩቤል ክንፎቻቸውን ወደ ላይ በመዘርጋት የስርየት መክደኛውን በድንፎቻቸው ጋረዱት። እርስ በርስ ትይዩ ሆነውም ወደ ስርየት መክደኛው መካከል ይመለከቱ ነበር። 10 ባስልኤል እርዝመቱ ሁለት ክንድ፣ ቁመቱም አንድ ተኩል ክንድ የሆነ ጠረጴዛ ከግራር ዕንጨት ሠራ። 11 ወርቅ ለበጠው፤ ዙሪያውንም በንጹሕ ወርቅ ከፈፈው። 12 አንድ ስንዝር ጠርዝ ከወርቅ ክፈፍ ጋር አበጀለት። 13 የወርቅ ቀለበቶችንም ሠርቶ የጠረጴዛው እግሮች ካሉበት ማእዘኖች ጋር አያያዛቸው። 14 ለመሸከም መሎጊያዎችን ማስገባት እንዲቻል ቀለበቶቹ ከጠርዙ ጋር ተያይዘው ነበር። 15 ጠረጴዛውን መሸከም እንዲቻል መሎጊያዎቹን ከግራር ዕንጨት ሠርቶ በወርቅ ለበጣቸው። 16 በጠረጴዛው ላይ የሚቀመጡ ዕቃዎችን፦ ድስቶችን፣ ዝርግና ጎድጓዳ ሳሕኖችን ጭልፋዎችን፣ ወጭቶችንና የመጠጥ መሥዋዕቱን ማፍሰሻ ማንቆርቆሪያዎች ከንጹሕ ወርቅ ሠራ። 17 ከነማቆሚያውና ከነዘንጉ ከተቀጠቀጠ ንጹሕ ወርቅ ሠራ። ጽዋዎቹ፣ ቀንበጦቹና አበባዎቹ በሙሉ ከመቅረዙ ጋር ወጥ ሆነው ነበር የተሠሩት። 18 ቅርንጫፎች በመቅረዙ አንድ ጎን፣ ሦስት ቅርንጫፎች ደግሞ በሌላው የመቅረዙ ጎን ተሠርተው ስድስት ቅርንጫፎች ነበር። 19 ቅርንጫፍ ከቀንበጥና ክአበባ ጋር የለውዝ አበባ የሚመስሉ ሦስት ጽዋዎች ነበሩት፤ በሌላውም ቅርንጫፍ እንደዚሁ የለውዝ አበባ የሚመስሉ ሦስት ጽዋዎች ከቀንበጥና ከአበባ ጋር ነበር። ከመቅረዙ ለሚወጡ ስድስት ቅርንጫፎች ሁሉ የተደረገው አንድ ዐይነት ነበር። 20 በመቅረዙ መካከል ላይ ባለው ዘንግ ላይ የለውዝ አበቦችን የሚመስሉ እራት ጽዋዎች ከቀንበጦቻቸውና ከአበቦቻቸው ጋር ተሠርተዋል። 21 በመጀመሪያ የቅርንጫፎች ጥንድ ሥር ወጥ ሆኖ ዐብሮት የተሠሩ ቀንበጦች ነበር። ከመቅረዙ በሚወጡ ስድስት ቅርንጫፎች ሁሉ የተደረገው አንድ ዐይነት ነበር። 22 ቅርንጫፎቻቸው ከመቅረዙ ጋር ወጥ ሆነው ከተቀጠቀጠ ንጹሕ ወርቅ የተሠሩ ነበር። 23 መቅረዙንና ሰባቱን መብራቶች፣ መኮስተሪያዎቹንና የኵስታሪ ማስቀመጫዎቻቸውን ከንጹሕ ወርቅ ሠራ። 24 መቅረዙንና ዐባሪ ዕቃዎቹን ከአንድ መክሊት ንጹሕ ወርቅ ሠራቸው። 25 እርዝመቱ አንድ ክንድ፣ ወርዱም አንድ ክንድ የሆነውን የዕጣኑን መሠዊያ ከግራር ዕንጨት ሠራ። አራት ማእዘንና ቁመቱም ሁለት ክንድ ነበር። ቀንዶቹም ከእርሱ ጋር ወጥ ሆነው የተሠሩ ነበር። 26 የዕጣኑን መሠዊያ፦ ዐናቱን፣ ጎኖቹንና ቀንዶቹን በንጹሕ ወርቅ ለበጣቸው። ለዙሪያውም የወርቅ ክፈፍ አበጀለት። 27 በሁለቱ ተነጻጻሪ ጎኖቹ ላይ ከክፈፉ ሥር እንዲያያይዙት ሁለት የወርቅ ቀለበቶችን ሠራ። ቀለበቶቹ መሠዊያውን ለመሸከም መሎጊያዎችን ለመያዝ የሚያገለግሉ ናቸው። 28 ከግራር ዕንጨት ሠርቶ በወርቅ ለበጣቸው። 29 የተቀሰውን የመቅቢያ ዘይትና የሽቶ ቀማሚ ሥራ የሆነውን፣ ንጹሕና ጣፋጭ መዐዛ ያለውን ዕጣን ሠራ።



Exodus 37:1

• ርዝመቱም ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል

ርዝመቱ 1.1 ሜትር፤ ስፋቱና ከፍታው 0.7 ሜትር ያህል ነው

• በአራቱ እግሮቹ ላይ አኖረ

እነዚህ እግሮች እንደሰው ወይም እንስሳ እግር የተቆጠሩ ሲሆን ታቦቱን የሚሸከሙ ወይም የሚደግፉ ናቸው።

Exodus 37:4

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው በማደሪያ ድንኳኑ ውስጥ የሚገኙ ቁሳቁሶችንና ሌሎችን በሚመለከት ዘጸአት 25፡13-14፥ 17 ተመልከት።

• ከጥሩ ወርቅም . . . ሠራ

የሠራው መሪ ባስልኤል በመሆኑ ሥራውን ብቻውን እንደሠራ አድርጎ ያቀርባል ነገር ግን ሥራው የተከናወነው ከሥራ ባልደረቦቹ ጭምር ነብር።

• ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፥ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የስርየት መክደኛ ሠራ

አንድ ክንድ በሜትር ሲለካ ከ46-50 ሳንቲ ሜትር ሲሆን ወደ ሜትር ሲቀየር 115 ሴ.ሜትር እና 70 ሳ.ሜ ያህል ነው።

Exodus 37:7

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው የሥርየት መክደኛው አሠራር በሚመለከት (37፡7-9) ዘጸአት 25፡18-20 ያለውን ክፍል እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት።

• በአንድ ላይ ሠራቸው

እርሱ እነዚህን አንድ አድርጎ ሠራቸው

• ኪሩቤልም ክንፎቻቸውን ወደ ላይ የዘረጉ ሆኑ፥ የስርየት መክደኛውንም በክንፎቻቸው ሸፈኑ

የክሩቤል ምስሎችን እውነተኛ ክሩቤል በማስመሰል ክንፎቻቸውን ዘርግተው አንዱ ከሌላው ጋር ተገናኝተውና የስርየት መደኛውን ሸፍነው እንዲቀመጡ አደረጋቸው። አማራጭ ትርጉም፦ ባስልኤል እነዚህን ክንፍ ያላቸውን ፍጥረታት የአንዱ ክንፍ ከሌላው ጋር እንድገናኙ አድርጎና ክንፎቻቸውን የዘረጉ እንዲሆኑ አድርጎ ሠራቸው።

• እርስ በርሳቸውም ተያዩ

የክሩቤል ዓይኖች አንዱ ሌላውን እንዲመለከቱ ተደርገው የተሰሩ ናቸው

Exodus 37:10

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው ምዕራፍ 37፡10-13 ያለውን ክፍል ከምዕራፍ 25፡23-26 ካለው ክፍል ጋር በማነጻጸር በተገቢው መንገድ ለመተርጎም ሞክር።

• ርዝመቱ ሁለት ክንድ፥ ወርዱም አንድ ክንድ፥ ቁመቱም አንድ ክንድ ተኩል

ርዝመቱ 92 ሴ.ሜትር፤ ወርዱ 46 ሴ.ሜትር እና ቁመቱ 69 ሴ.ሜትር ያህል ነበር

• አንድ ጋት

በባህላዊው ልከት አንድ ጋት የአራት ጣቶች ጥምር ማለት ሲሆን ከ8-10 ሳ.ሜትር ነው።

• አራቱ እግሮቹ

እነዚህ እግሮች እንደሰው ወይም እንስሳ እግር የተቆጠሩ ሲሆን ታቦቱን የሚሸከሙ ወይም የሚደግፉ ናቸው።

Exodus 37:14

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው ምዕራፍ 37፡14-16 ያለውን ክፍል ከምዕራፍ 25፡27-29 ካለው ጋር በማነጻጸር ተገቢውን የትርጉም ሂደት በመከተል መልዕክቱን ተርጉም።

• ቀለበቶች በክፈፉ አቅራቢያ ነበሩ

“ቀለበቶች ከክፈፉ ጋር ተያይዘው ተሰሩ ወይም ቀለበቶችን ከክፈፉ ጋር አያይዘው ሰሩ”

• ወጭቶቹንና ጭልፋዎቹን ጽዋዎቹንም መቅጃዎቹንም

ዝርግ ሳህኖችን፥ ድስቶችን፥ ጎድጓዳ ሳህኖችን (ውሃ መያዣዎችን) እና ማንቆርቆሪያዎችን . . .

Exodus 37:17

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው ምዕራፍ 37፡17-19 ያለውን ክፍል ከምዕራፍ 25፡31-33 ካለው ጋር በማነጻጸር ተገቢውን የትርጉም ሂደት በመከተል መልዕክቱን ለመተርጉም ሞክር።

• ጽዋዎቹን፥ ጕብጕቦቹን፥ አበቦቹን ከዚያው በአንድነት አደረገ

የአበባ ቅርጽ ያላቸው ጽዋዎችን፥ እንቡጦችንና የፈኩ አበቦችን አንድ ወጥ አድርጎ ሠራቸው

• ጕብጕቡንና አበባውን ሦስትም የለውዝ አበባ የሚመስሉትን ጽዋዎች

ከእንቡጦችና ከፈኩ አበቦች ጋር የለውዝ አበባ የሚመስሉ ሶስት ጽዋዎች

• የለውዝ አበባ

ነጭ ወይም ሮዝ መልክ ያለው የለውዝ አበባ በለውዝ ዘፍ ላይ ያደገ የሚመስል ነበር

Exodus 37:20

በዚህ ክፍል ያሉ ቃላትና ዕቃዎችን እንዴት እንደተርጎምክ በምዕራፍ 25፡34-36 ተመልከት።

በዚህ ክፍል ያሉ ቃላትና ዕቃዎችን እንዴት እንደተርጎምክ በምዕራፍ 25፡34-36 ተመልከት።

• በመቅረዙም ጕብጕቦቹንና አበቦቹን

በመቅረዙ ላይ እንቡጦችና አበቦች አደረገ

• አራትም የለውዝ አበባ የሚመስሉትን ጽዋዎች አደረገ

የለውዝ አበባ የሚመስሉ አራት ጽዋዎች ወይም ስኒዎች አደርገ ወይም ሰራ

• አንድ ሆኖ የተሠራ አንድ ጕብጕብ

ከመቅረዙ ጋር አንድ ወጥ ሆነው የተሰሩ እንቡጦች

Exodus 37:23

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው በዚህ ክፍል የተጠቀሱ ቃላትና ቁሶችን እንዴት እንደተረጎምክ በ25፡37-39 ላይ ተመልከት

• መኰስተሪያዎቹንም፥ የኩስታሪ ማድረጊያዎቹንም

እነዚህ መኮስተሪያዎች ሁለት ሆነው ከብረት ወይም ከእንጨት የተሰሩ ሲሆን በአንድ በኩል የተያያዙ ናቸው፥ ዕቃዎችን ቆንጥጦ ለመያዝና ለማውጣት የሚያገለግሉ እንደ መቆንጠጫ ያሉ ናቸው።

• ከአንድ መክሊት ጥሩ ወርቅ አደረገ

x

Exodus 37:25

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው የዚህን ክፍል (37፡25-26) ትርጉም ከምዕራፍ 30፡1-3 ካለው ጋር አነጻጽር

• ቀንዶቹም ከእርሱ ጋር በአንድነት የተሠሩ ነበሩ

ቀንዶቹ ከመሰዊያው ጋር በአንድ ላይ ተያይዘው የተሰሩ ናቸው

Exodus 37:27

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የማደሪያውን ድንኳንና በውስጡ የሚገኙ ሥራዎችን ስለመሥራታቸው የዚህን ክፍል (37፡27-28) ትርጉም ከምዕራፍ 30፡4-5 ካለው ጋር አነጻጽር

• ጥሩውንም የጣፋጭ ሽቱ ዕጣን በቀማሚ ብልሃት

የሽቱ ቀማሚ ሥራ የሆነውን ንጹህና መልካም መዓዛያለውን ዕጣን


Chapter 38

1 የሚቃጠለውን መሥዋዕት መሠዊያ ከግራር ዕንጨት ሠራ። ዐምስት ክንድ እርዝመትና ዐምስት ክንድ ስፋት፣ አራት ማእዘንና ሦስት ክንድ ቁመት ነበረው። 2 ማእዘኖችም የበሬ ቀንዶችን የሚመስሉ ቅርጾችን በመሥራት አስረዘማቸው። ቀንዶቹ ከመሠዊያው ጋር ወጥ ሆነው የተሠሩ ነበሩ፤ መሠዊያውንም በነሐስ ለበጠው። 3 ለመሠዊያው የሚያስፈልገውን ዕቃ ሁሉ፦ ለዐመድ ምንቸቶችን፣ መጫሪያዎችን፣ ጎድጓዳ ሳሕኖችን፣ ሜንጦዎችንና ማንደጃዎችን በሙሉ ከነሐስ ሠራ። 4 ከደረጃው ሥር ከመሠዊያው እኩሌታ እስከ ታች የሚደርስ እንደ መረብ የተሠራ የነሐስ ፍርግርግ ለመሠዊያው አበጀ። 5 ፍርግርግ አራት ማእዘኖች ለመሎጊያዎቹ መያዣ አራት ቀለበቶችን ሠራላቸው። 6 ዕንጨት መሎጊያዎችን ሠርቶ በነሐስ ለበጣቸው። 7 መሎጊያዎቹን መሠዊያውን ለመሸከም በመሠዊያው ጎኖች ላይ ባሉት ቀለበቶች ውስጥ አስገባቸው። መሠዊያውን ክፍት አድርጎ በሳንቃዎች ሠራው። 8 ባስልኤል ትልቁን የመታጠቢያ ሳሕን ከነሐስ መቆሚያ ጋር ሠራ። ሳሕኑን የሠራውም በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ የሚያገለግሉት ሴቶች ይጠቀሙባቸው ከነበሩ መስተዋቶች ነው። 9 ሠራው። በአደባባዩ ደቡብ ጎን ላይ የነበሩት መጋረጃዎች ከአማረ በፍታ የተሠሩና አንድ መቶ ክንድ እርዝመት ያላቸው ነበሩ። 10 መጋረጃዎቹ ሃያ ምሰሶዎችና ሃያ መቆሚያዎች ነበሯቸው። ከምሰሶዎቹና ከብር ዘንጎቹ ጋር የተያያዙ ኵላቦችም ነበሩ። 11 ጎን በኩልም እንደዚሁ አንድ መቶ ክንድ እርዝመት ያላቸው መጋረጃዎች ከሃያ ምሰሶዎችና ከሃያ የነሐስ መቆሚያዎች፣ ከምሰሶዎቹ ጋር ከተያያዙ ኲላቦችና ከብር ዘንጎች ጋር ነበር። 12 የምዕራቡ ጎን መጋረጃዎች ዐምሳ ክንድ የሚረዝሙ፣ ዐሥር ምሰስዎችና መቆሚያዎች ያሏቸው ነበሩ። የምሰሶዎቹ ኵላቦችና ዘንጎች ብር ነበሩ። 13 አደባባዩም በምሥራቁ ጎን ላይ ዐምሳ ክንድ ይረዝም ነበር። 14 የመግቢያው አንድ ጎን መጋረጃዎች እርዝመት ዐሥራ ዐምስት ክንድ ነበረ። ሦስት ምሰሶዎች ከሦስት መቆሚያዎች ጋር ነበሯቸው። 15 በአደባባዩ መግቢያ ሌላ ጎን ላይም ዐሥራ ዐምስት ክንድ የሚረዝሙና ሦስት ምሰሶዎችና ሦስት መቆሚያዎች ያሏቸው መጋረጃዎች ነበሩ። 16 በአደባባዩ ዙሪያ ያሉት መጋረጃዎች ሁሉ አምሮ ከተፈተለ በፍታ የተሠሩ ነበሩ። 17 የምሰሶዎቹ መቆሚያዎች ከነሐስ፣ የምሰሶዎቹ ኵላቦችና ዘንጎቻቸው፣ የዐናታቸውም መሸፈኛ ከብር የተሠሩ ነበሩ። የአደባባዩ ምሰሶዎች ሁሉ በብር የተለበጡ ነበር። 18 የአደባባዩ በር መጋረጃቅ እርዝመት ሃያ ክንድ ነበረ። ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና አምሮ ከተፈተለ በፍታ የተሠራ ነበረ። እንደ አደባባዩ መጋረጃዎች ሃያ ክንድ እርዝመትና ዐምስት ክንድ ቁመት ነበረው። 19 የነሐስ መቆሚያዎችና የብር ኵላቦች ነበሩት። የዐናታቸው መሸፈኛና ዘንጎቹ ከብር የተሠሩ ነበሩ። 20 የመገናኛው ድንኳን ካስማዎች ሁሉ የተሠሩት ከነሐስ ነበር። 21 የሙሴን ትእዛዝ በመከተል በተመዘገበው መሠረት የመገናኛው ድንኳን፣ ይኸውም የምስክሩ ድንኳኝ ቆጠራ ይህ ነው። በካህኑ በአሮን ልጅ በኢታማር መሪነት ይህ የሌዋውያኑ ሥራ ነበረ። 22 ከይሁዳ ነገድ የሆነው፣ የሖር የልጅ ልጅ፣ የኡሪ ልጅ ባስልኤል እግዚአብሔር ለሙሴ የሰጠውን ትእዛዝ ሁሉ ፈጸመ። 23 ከባስልኤልም ጋር ከዳን ነገድ የሆነው የአሂሳሚክ ልጅ ኤልያብ ቅርጽ አውጪ ሠራተኛ፣ የእጅ ጥበብ ሙያተኛ፣ በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ግምጃና በአማረ በፍታ ጥልፍ ጠላፊም ሆኖ ዐብሮት ሠራ። 24 ከመቅደሱ ሥራ ጋር ለተያያዘው ተግባር ሁሉ ጥቅም ላይ የዋለው ወርቅ ማለትም፣ ከስጦታው የተገኘው ወርቅ ሁሉ በመቅደሱ ሰቅል መጠን መሠረት ሃያ ዘጠኝ መክሊትና ሰባት መቶ ሠላሳ ሰቅል ነበረ። 25 ማኅበረ ሰቡ የሰጠው ብር በመቅደሱ ሰቅል መጠን ተመዝኖ አንድ መቶ መክሊትና አንድ ሺሕ ሰባት መቶ ሰባ ዐምስት ሰቅል፣ 26 በአንድ ሰው አንድ ቤካ ይኸውም በመቅደሱ ሰቅል መጠን ግማሽ ሰቅል ነበረ። ይህ ቍጥር የተደረሰበት በሕዝብ ቆጠራው ሃያ ዓመትና ከዚያም በላይ የሆናቸው ተቆጥረው በተገኘው ስድስት መቶ ሦስት ሺሕ ዐምስት መቶ ዐምሳ ወንዶች ቍጥር በያንዳንዱ ሰው ተሰልቶ ነው። 27 የመቅደሱንና የመጋረጃዎችን መቆሚያዎች ለመሥራት አንድ መቶ የብር መክሊት ወጪ ሆኖአል፦ መቆሚያዎቹ በጠቅላላ አንድ መቶ ሆነው፣ ለያንዳንዱ መቆሚያ አንድ መክሊት ተከፍሎአል ማለት ነው። 28 በቀሩት አንድ ሺሕ ሰባቶ መቶ ሰባ ዐምስት የብር ሰቅሎች ባስልኤል የምሰሶዎቹን ኵላቦች ሠርቶ ዐናታቸውን ሸፈነባቸው፤ ዘንጎችንም ለምሰሶዎቹ ሠራባቸው። 29 ከስጦታ የተገኘው ነሐስ ተመዝኖ ሰባ ታለንትና ሁለት ሺሕ አራት መቶ ሰቅል ሆነ። 30 በዚህም የመገናኛውን ድንኳን መግቢያ መቆሚያዎች፣ የነሐስ መሠዊያውን፣ የእርሱንም የነሐስ ፍርግርግ፣ የመሠዊያውን ዕቃ ሁሉ፣ 31 የአደባባዩን መቆሚያዎች፣ የአደባባዩን መግቢያ መቆሚያዎች፣ የመገናኛውን ድንኳንና የአደባባዩን ድንኳን ካስሞች ሁሉ ሠራበት።



Exodus 38:1

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የመገናኛውን ድንኳንና የውስጡን ቁሳቁስ ሥራ ይቀጥላሉ።

• ዕቃውንም ሁሉ ከናስ አደረገ

የእነዚህ ዕቃዎች ዝርዝርና ፍቺያቸውን እንዴት እንደተረጎምክ ዘጸአት 27፡1-3 ካለው ክፍል ጋር አነጻጽር።

• ርዝመቱ አምስት ክንድ፥ ወርዱም አምስት ክንድ . . . ከፍታው ሦስት ክንድ ነበረ

ርዝመቱ 2.30 ሜትር፥ ስፋቱ 2̄.30 ሜትር እና ቁመቱ 1.38 ሜትር ነበር

• ቀንዶቹም ከእርሱ ጋር በአንድ የተሠሩ ነበሩ

ቀንዶቹ ከመሠዊያው ጋር አንድ ወጥ ሆነው የተሠሩ ነበሩ

Exodus 38:4

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የመገናኛውን ድንኳንና የውስጡን ቁሳቁስ ሥራ ይቀጥላሉ። ምዕራፍ 38፡4-5 ያለውን ክፍል ለመተርጎም ምዕራፍ 27፡4-5 ያለውን ክፍል እንዴት እንደተረጎምክ አነጻጽር።

Exodus 38:6

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የመገናኛውን ድንኳንና የውስጡን ቁሳቁስ ሥራ ይቀጥላሉ

• ከሳንቆቹም ሠርቶ ባዶ አደረገው

መሠዊያው ከሳንቃ (ጠፍጣፋ የሆነ) የተሠራ ሆኖ ውስጡ ክፍት ነበር (ዘጸአት 27፡7-8 ተመልከት)

Exodus 38:8

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የመገናኛውን ድንኳንና የውስጡን ቁሳቁስ ሥራ ይቀጥላሉ

• የመታጠቢያውን ሰንና መቀመጫውንም

“መቀመጭው” የመታጠቢያው ሳህን የሚቀመጥበት ነው። አማራጭ ትርጉም፦ “የመታጠቢያውን ሳሕንና ማስቀመጫውን ጭምር ከነሐስ ሠራ” ዘጸአት 30፡18 ተመልከት።

• ከሴቶች መስተዋት ከናስ አደረገ

የነሐስ ብረቱ ከመስተዋት የተገኘ (የመጣ) ነበር። የመታጠቢያ ሳህኑ የተሰራው ከመስተዋት ነበር። ይህ መስተዋት ሴቶች ካመጡት የነሐስ መስተዋቶች የተሰራ ነበር።

• መስተዋት

አንጻባራቂና ሰዎች ፊታቸውን ወይም ሌሎችን ነገሮች ለማየት የሚጠቀሙት የብረት ቁራጭ ነው

Exodus 38:9

አጠቃላይ ምልከታ፦

ባስልኤልና የሥራ ጓደኞቹ የመገናኛውን ድንኳንና የውስጡን ቁሳቁስ ሥራ ይቀጥላሉ

• የተፈተለ የጥሩ በፍታ መጋረጆች ነበሩ

ይህን ክፍል ለመተርጎም ይረዳህ ዘንድ ዘጸአት ምዕራፍ 27፡9-10 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት

• ርዝመቱ መቶ ክንድ የሆነ

ርዝመቱ 46 ሜትር ወይም 4600 ሴ. ሜትር የሆነ

Exodus 38:11

ይህን ክፍል ለመተርጎም ይረዳህ ዘንድ ዘጸአት ምዕራፍ 27፡11-12 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት

ይህን ክፍል ለመተርጎም ይረዳህ ዘንድ ዘጸአት ምዕራፍ 27፡11-12 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት

• መቶ ክንድ ርዝመት . . . አምሳ ክንድ ርዝመት . . .

46 ሜትር ርዝመት . . . 23 ሜትር ርዝመት

Exodus 38:13

• በምሥራቅም ወገን . . . ዙሪያ

ይህን ክፍል ለመተርጎም ይረዳህ ዘንድ ዘጸአት ምዕራፍ 27፡13-16 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት። የመግቢያው ደጅ ባለበት በምሥራቅ በኩልና በድንኳኑ መግቢያ ዙሪያ ያሉት መጋረጃዎች።

• መጋረጆች ሁሉ ከተፈተለ ከጥሩ በፍታ ተሠርተው ነበር

ባስልኤልና ሌሎች የሥራ ባልደረቦቹ መጋረጃዎችን ከጥሩ በፍታ (ሐር) ሰርተውት ነበር።

Exodus 38:17

ይህን ክፍል ለመተርጎም ይረዳህ ዘንድ ዘጸአት ምዕራፍ 27፡16-19 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት።

ይህን ክፍል ለመተርጎም ይረዳህ ዘንድ ዘጸአት ምዕራፍ 27፡16-19 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት።

• የምሰሶቹም እግሮች የናስ

ባስልኤልና የሥራ ባልደረቦቹ የምሰሶዎቹ እግሮች የሠረኡትከነሐስ ብረት ነበር።

• ጉልላቶቹና ዘንጎቹም በብር ተለብጠው ነበር

ባስልኤልና የሥራ ባልደረቦቹ /ጓደኞቹ/ ጫፎቻቸውንና ዘንጎቻቸውን ከብር ሠርተውት ነበሩ

Exodus 38:21

አገናኝ ሀረግ፦

ባስልኤልና የሥራ ባልደረቦቹ የማደሪያ ድንኳኑንና በውስጡ ያሉ ቁሶችን ቀጥለው ሠሩ

• በኢታማር እጅ እንደ ተቈጠረው የማደሪያው፥ የምስክሩ ማደሪያ፥ ዕቃ ድምር ይህ ነው

በኢታማር መሪነት በሌዋውያን ሀላፊነት የተቆጠረሩ የመገናኛው ድንኳን ዕቃዎች ዝርዝር ቈጠራ ይህ ነው

• እግዚአብሔር ለሙሴ ያዘዘውን ሁሉ አደረገ

እግዚአብሔር በሙሴ በኩል ያዘዛቸውን ነገሮች ሁሉ ሠሩ።

• ኢታማር፥ ባስልኤል፥ ሆር፥ ኡር

እነዚህ የወንዶች ስም ዝርዝር ነው

• የአሂሳሚክ ልጅ ኤልያብ ነበረ

እነዚህ የወንዶች ስም ዝርዝር ነው

• የቅርጽ ሠራተኛና ብልህ ሠራተኛ

አንጥረኛ (የእጅ ጥበብ ባለሙያ) እና ፕላን (ዕቅድ) አውጪ ባለሞያ

Exodus 38:24

• የተሰጠው ወርቅ ሁሉ

ሰዎች ለሥራው የሠጡት ወርቅ በሙሉ

• ሀያ ዘጠኝ መክሊት ሰባት መቶ ሠላሳ ሰቅል ነበረ

አንድ መክሊት 33 ኪሎ ግራም ሲሆን 29 መክሊት 960 ኪሎ ግራም ወርቅ እና አንድ ሰቅል 3.3 ክሎ ግራም ሲሆን 100 ሰቅል 330 ኪሎ ግራም ይሆናል። በጠቅላላው የወርቁ ቁጥር 1290 ኪሎ ግራም ወርቅ ነበር።

• መቶ መክሊትና አንድ ሺህ ሰባት መቶ ከሰባ አምስት ሰቅል ብር

በጠቅልላው 1775 ሰቅል ወይም 5858 ኪሎ ግራም ብር ነበር

• የሰቅል ግማሽ (አንድ ቤካ)

አንድ ሰቅል 11 ግራም ሲሆን የሰቅል ግማሽ 5.5 ግራም ይሆናል።

• ከተቈጠረው ከእያንዳንዱ ሰው የተሰጠ ነው

ይህ የሰቅል ግማሽ የተሰበሰበው ዕድሜያቸው 20 አመት የሆናቸው፥ በቆጠራው የተካተቱና ግማሽ ሰቅል (አንድ ቤካ) መስጠት የሚገባቸው ሰዎች ቁጥር ማለት ነው።

• እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን

የቤተመቅደስ የሰቅል ሚዛን ደረጃውን የጠበቀ ስለሆነ “በተቀደሰ ሚዛን፤ በታወቀው ሚዛን” ይባላል።

Exodus 38:27

• መቶውም የብር መክሊት

3300 ኪሎ ግራም የሚመዝን ብር

• ሺህ ሰባት መቶ ሰባ አምስት ሰቅል

ወደ 20 ኪሎ ግራም የሚመዝን

• ሰባ መክሊትና ሁለት ሺህ አራት መቶ ሰቅል

በጠቅላላው 2300 ክሎ ግራም የሚመዝን የነሐስ ብረት ነበር

Exodus 38:30

• የናሱን መከታ

ከነሐስ ብረት የተሰራ ሲሆን እንጨት በእሳት ሲቃጠል ለመያዝ የሚያገለግል (ዘጸአት 27፡4 ተመልከት)

• የማደሪያውንም ካስማዎች

ከእንጨት ወይም ከብረት የተሰሩ የድንኳን ጠርዞችን ወይም ማዕዘኖችን ለመወጠር የሚያገለግሉ ናቸው (ዘጸአት 27፡19 ተመልከት)


Chapter 39

1 በመቅደሱ ውስጥ ለሚከናወነው አገልግሎት ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ የተሠሩ ልብሶችን አበጁ። እግዚአብሔር ሙሴን ባዘዘው መሠረት ለቤተ መቅደሱ የሚሆኑ የአሮንን ልብሶች ሠሩ። 2 ኤፉዱን ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና አምሮ ከተፈተለ በፍታ ሠራ። 3 ሠራተኛ እንደሚሠራው፣ በሰማያዊ፣ በሐምራዊ፣ በቀይ ማግና በአማረ በፍታ ለመ|ሥራት ወርቁን ቀጥቅጠው ወደ ሽቦነት ቆራረጡት። 4 የትከሻ ንጣዮችን ሠርተው ከላይኛዎቹ ጠርዞቹ ጋር አያያዙት። 5 በብልኀት የተጠለፈው የወገብ መታጠቂያም እንደ ኤፉዱ ሲሆን፣ እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘው፣ አምሮ ከተፈተለ በፍታ ይኸውም ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ ከኤፉድ ጋር ወጥ ሆኖ የተሠራ ነበረ። 6 የመረግድ ድንጋዮችን በወርቅ ፈርጥ ክፈፍ አበጁላቸው፤ እንደ ማኅተምም የዐሥራ ሁለቱን የእስራኤል ልጆች ስሞች ቀረጹባቸው። 7 እግዚአብሔር ሙሴን ባዘዘው መሠረት፣ ባስልኤል በሴፉዱ የትከሻ ንጣዮች ላይ ለዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ልጆች የመታሰቢያ ድንጋዮች አድርጎ አስቀመጣቸው። 8 ኪሱንም ብልኅ ሠራተኛ እንደሚሠራው፣ እንደ ኤፉዱ አበጀው። ከወርቅ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊ፣ ከቀይ ማግና ከአማረ በፍታ ሠራው። 9 ኪሱ አራት ማእዘን ነበረ። ርዝመቱም ወርዱም አንድ ስንዝር ሆኖ የተደረበ ዕጥፍ ነበረ። 10 በውስጡም አራት የዕንቍ ድንጋዮች ፈድፎች አበጅተዋል። በመጀመሪያው ረድፍ ሰርድዮን፣ ቶጳዝዮንና አብራቅራቂ ዕንቍ ነበሩት። 11 ረድፍ በሉር፣ ሰንፔር፣ አልማዝ፤ 12 በሦስተኛው ረድፍ ያክንት፣ ኬልቄዶን፣ አሜቴስጢኖስ፤ 13 በአራተኛውም ረድፍ ቢረሌ፣ መረግድና ኢያስጲድ ነበሩ። ድንጋዮቹ በወርቅ ፈርጥ ዙሪያቸውን የተከፈፉ ነበር። 14 እያንዳንዳቸው በዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ልጆች ስሞች ቅደም ተከተል መሠረት የተቀመጡ ነበር። እያንዳንዱ ስም ከዐሥራ ሁለቱ ነገዶች አንዱን በመወከል በማተሚያ ቀለበት ላይ እንደሚቀረጽ የተቀረጸባቸው ነበሩ። 15 ኪሱ ላይ ከንጹሕ ወርቅ እንደ ገመድ የተጎነጎኑ ድሪዎችን አበጁ። 16 ሁለት የወርቅ ፈርጦችንና ሁለት የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተው ሁለቱን ቀለበቶች ከደረት ኪሱ ሁለት ጠርዞች ጋር አያያዟቸው። 17 ሁለቱን የተጎነጎኑ የወርቅ ድሪዎች በደረት ኪሱ ጠርዞች ሁለት ቀለበቶች ውስጥ አስቀመጧቸው። 18 ሌሎች ሁለት ጫፎች ከሁለት ፈርጦች ጋር አያያዟቸው። ከኤፉዱ የትከሻ ንጣዮች ጋር በኤፉዱ ፊት አገናኗቸው። 19 የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተው ከውስጠኛው ጠርዝ ቀጥሎ በሚገኘው ጎን በደረት ኪሱ ሌሎች ሁለት ጠርዞች ላይ አስቀመጧቸው። 20 ተጨማሪ የወርቅ ቀለበቶችን ሠርተው፣ በመያዣው አጠገብ በብልኀት ከተሠራው የወገብ መታጠቂያ በላይ፣ ከአፉዱ ፊት ሁለት የትከሻ ንጣዮች ግርጌ ጋር አያያዟቸው። 21 በብልኀት ከተሠራው ከኤፉዱ የወገብ መታጠቂያ በላይ መያያዝ እንዲችል፣ የደረት ኪሱን በራሱ ቀለበቶች ከኤፉዱ ቀለበቶች ጋር በሰማያዊ ፈትል አሰሩት። ይህ የሆነው የደረት ኪሱ ከኤፉዱ የተነጠለ እንዳይሆን ነው። የተደረገውም እግዚአብሔር ሙሴን አዝዞት በነበረው መሠረት ነው። 22 የኤፉዱን ቀሚስ ሙሉ በሙሉ የሸማኔ ሥራ ከሆነው ከሐምራዊ ጨርቅ ሠራው። 23 መካከሉ ላይ ዐንገት ማስገቢያ ነበረው። እንዳይቀደድም ዙሪያውን የተዘመዘመ ጠርዝ ነበረው። 24 በታችኛው የቀሚሱ ዘርፍ ላይም የሰማያዊ፣ የሐምራዊ፣ የቀይ ማግና የአማረ በፍታ ሮማኖችን አበጁ። 25 ሻኵራዎችን ከንጹሕ ወርቅ ሠርተው በታችኛው የቀሚሱ ጠርዝ ዙሪያ ላይ በሮማኖቹም መካከል፣ 26 አገልግሎት በቀሚሱ ጠርዝ ላይ ሻኵራን ሮማን፣ ሻኵራና ሮማን እያደረጉ አስቀመጧቸው። ይህም የሆነው እግዚአብሔር ሙሴን አዝዞት በነበረው መሠረት ነው። 27 ለአሮንና ለልጆቹ ሸሚዞችን ከአማረ በፍታ ሠሩ። 28 የራስ መጠምጠሚያዎችን፣ ቆቦችንና ሱሪዎችን ከአማረ በፍታ፣ 29 መታጠቂያዎችንም ከአማረ በፍታ፣ ከሰማያዊ፣ ከሐምራዊና ከቀይ ማግ ጥልፍ ጠላፊ እንደሚሠራው አድርገው አበጇቸው። ይህም የሆነው እግዚአብሔር ሙሴን አዝዞት በነበረው መሠረት ነው። 30 አክሊል ሠሌዳ ከንጹሕ ወርቅ ሠርተው በቀለበት ላይ ማኅተም እንደሚቀረጽ በላዩ ቅዱስ ለእግዚአብሔርን ቀረጹበት። 31 እግዚአብሔር ሙሴን አዝዞት እንደ ነበረው፣ በመጠምጠሚያው ዐናት ላይ ለማንጠልጠል ሰማያዊ ፈትል አሰሩበት። 32 ድንኳን፣ የማደሪያው ሥራ ተጠናቀቀ። የእስራኤል ሰዎች እግዚአብሔር ለሙሴ የሰጣቸውን መመሪያዎች በመከተል ሁሉንም አደረጉ። 33 ድንኳኑንና ዕቃዎቹን ሁሉ፣ ካስማዎቹን፣ ወጋግራዎቹን፣ አግዳሚዎቹን፣ ምሰሶዎቹንና መቆሚያዎቹን፣ 34 በቀይ ቀለም የተነከረውን የአውራ በግ ቆዳ መሸፈኛ፣ የአስቆጣ ቆዳዊን መሸፈኛና የሚሸፍነውን መጋረጃ፣ 35 የምስክሩን ታቦት፣ መሎጊያዎቹንና የስርየት መክደኛውን ወደ ሙሴ አመጡ። 36 ጠረጴዛውን፣ የጠረጴዛውን ዕቃዎች ሁሉና የገጽ ኅብስቱን፤ 37 የንጹሑን ወርቅ መቅረዝና የረድፍ መብራቶችን ከዐባሪ ዕቃዎቹና ከመብራቶቹ ዘይት ጋር፤ 38 መሥዐዊያውን፣ መቅቢያ ዘይቱንና ጣፋጭ መዐዛ ያለን ዕጣን፣ የመገናኛውን ድንኳን መግቢያ መጋረጃ፤ 39 የነሐስ መሠዊያውን ከነሐስ ፍርግርጉና ከመሎጊያዎቹ፣ ከዕቃዎቹ፣ ከትልቁ የመታጠቢያ ሳሕንና ከመቆሚያው ጋር አመጡ። 40 የአደባባዩን መጋረጃዎች ከምሰሶዎቹና ከመቆሚያዎቹ ጋር፣ የአደባባዩን መግቢያ መጋረጃም፣ ገመዶቹንና የድንኳን ካስማዎችን፣ ለመገናኛው ድንኳን አገልግሎት ጥቅም ላይ የሚውለውን ዕቃ ሁሉ አመጡ። 41 አገልግሎት በጥበብ የተሠሩትን ልብሶች፣ ካህናት ሆነው እንዲያገለግሉ የካህኑን የአሮንንና የልጆቹን የተቀደሱ ልብሶችም አመጡ። 42 ስለዚህም የእስራኤል ሰዎች እግዚአብሔር ሙሴን ባዘዘው መሠረት ሥራውን በሙሉ አከናወኑ። 43 ሙሴ ሥራውን ሁሉ ሲፈትሽ፣ እነሆ ሁሉን አከናውነውታል። ያከናወኑትም እግዚአብሔር አዝዞት በነበረው በዚያው መንገድ ነው። ሙሴም ሕዝቡን ባረካቸው።



Exodus 39:1

• የተቀደሰውን ልብስ አደረጉ

“አደረጉ” የሚለው ቃል ባስልኤል፥ ኤልያብና ማናቸውንም ሥራ ለመሥራት ችሎታንና ዕውቀትን የሰጣቸው ሌሎች ሰዎች ማለት ነው

• እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው

እነዚህ ሰዎች ሥራውን የሰሩት እግዚአብሔር ሙሴን ባዘዘው መሠረት ነው ማለት ነው።

Exodus 39:2

አጠቃላይ ምልከታ፦

በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• ባስልኤል

ይህ የሰው ስም ነው፤ ልንጽጽር ዘጸአት 31፡1-2 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት

Exodus 39:4

አጠቃላይ ምልከታ፦

በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• ሁለቱ ወገን እንዲጋጠም በሁለቱ ጫንቃዎች ላይ የሚጋጠም ልብስ አደረጉት

ለኤፉዱም ማንገቻ በትከሻ ላይ የሚወርዱ ሁለት ማንጠልጠያ ሠርተው ጐንና ጐኑ እንዲያያዙ አደረጉ

• እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው

እነዚህ ሰዎች ሥራውን የሰሩት እግዚአብሔር ሙሴን ባዘዘው መሠረት ነው ማለት ነው። ቁጥር 1 ተመልከት።

Exodus 39:6

አጠቃላይ ምልከታ፦

በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• የመረግድ ድንጋዮች ሠርተው

የመረግድ ድንጋዮችን ወስደው የወርቅ ፈርጥ ቅርጽ በድንጋዩ ላይ ቀርጸው እንደ ማለት ነው

• ለእስራኤል ልጆች የመታሰቢያ ድንጋዮች

በ12ቱ (በእስራ ሁለቱ) የእስራኤል ልጆች መታሰቢያ ይሆን ዘንድ ከድንጋይ የተቀረጸ

Exodus 39:8

አጠቃላይ ምልከታ፦

በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• አደረገው

አዲሱ አማርኛ እና መደበኛው አማርኛው ትርጉም “ሠሩት” ብሎ በወል ስም ይጠቅሳሉ። የዕብራይስጡ ቅጅ፥ የቀድሞ አማርኛ ቅጅና ለሎች ተአማኒነት ያላቸው ቅጅዎች “አደረገው” ይላሉ። “ሠሩት” በሚል የተረጎሙት ትኩረታቸው ባስልኤል፥ ኤልያብና ሌሎች ሰዎችን ታሳቢ በማድረግ ነው። “አደረገው” በሚል የተረጎሙት ትኩረታቸው የሥራው ዋና መሪ ባስልኤል ስለሆነ ትኩረታቸው በእርሱ ላይ ነው። የዕብራይስጡ ቅጅ ትኩረቱ በባስልኤል ላይ ስለሆነ “እርሱ አደረገው” የሚል ነው። ስለሆነም አደረገው የሚለው ትክክለኛ ትርጉም ነው።

• አንድ ስንዝር

በዘመናዊ የርቀት መለኪያ ከ20-22 ሴንቲ ሜትር ያህል ነው።

Exodus 39:10

አጠቃላይ ምልከታ፦

በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• ዕንቁዎቹንም በአራት ተራ አደረጉበት

ሠራተኞች የከበሩ ድንጋዮችን በተነገራቸው መሰረት በአራት ረድፍ አደርገው ሰሩት

• ሰርድዮን፥ ቶጳዝዮን …

የአነዚህን ድንጋዮች ስም ዝርዝር በየቋንቋው ለማግኘት አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን እነዚህ ዕንቁ የተባሉት “የከበሩ ወይም ውድ” የድንጋይ ዓይነቶች መሆናቸውና አንዱ ከሌላው የተለየ መሆኑን ማወቅ አስፈላጊ ነው። ስለሆነም በትርጉም ወቅት ተውሶ ወይም ባዕድ ቃላትን በመጠቀም ትርጉሙን ግልጽ ማድረግ ይቻላል።

• በወርቅ ፈርጥ ተደረጉ

እነዚህን የከበሩ ወይም ውድ ድንጋዮችን በወርቅ ፈርጥ ወይም በተቀረጸው ወርቅ ላይ አስቀመጡ

Exodus 39:14

አጠቃላይ ምልከታ፦

በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

Exodus 39:17

• የተጐነጐኑ የወርቅ ድሪዎች

ከንጹህ ወረቅ የተሰሩ የወርቅ ሰንሰለት ወይም ገመድ መሳይ

Exodus 39:19

አጠቃላይ ምልከታ፦

በምዕራፍ 28፡26-27 በተጠቀሰው መሰረት በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• የወርቅ ቀለበቶች ሠሩ

ለማያያዣነት የሚያገለግሉ የወርቅ ቀለበቶች ወይም ክብ ነገር

• በብልሃት ከተጠለፈው ቋድ

ከጨርቅ ወይም ከጨርቅ ክር የተሰራ የወገብ መታጠቂያ ወይም ቀበቶ ሲሆን የእጄ ጥበብ ባለሙያ የሰራው ዓይነት ማለት ነው

Exodus 39:21

አጠቃላይ ምልከታ፦

በምዕራፍ 28፡28 በተጠቀሰው መሰረት በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• ከኤፉዱም እንዳይለይ

ከኤፉዱ እንዳይላቀቅ የሚያደርግ ወይም በጥብቅ እንዲተሳሰር የሚያደርግ

Exodus 39:22

አጠቃላይ ምልከታ፦

በምዕራፍ 28፡31-33 በተጠቀሰው መሰረት በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• ባስልኤል

ይህ የሰው ስም ነው፤ ልንጽጽር ዘጸአት 31፡1-2 ላይ ስሞችን እንዴት እንደምትተረጉም አስተውል

Exodus 39:25

አጠቃላይ ምልከታ፦

በምዕራፍ 28፡34-35 ላይ በተሰጠው መመሪያ መሰረት በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• ከጥሩ ወርቅም ሻኵራዎችን

ከጥሩ ወርቅ ጸናጽሎችን ወይም ትናንሽ ድምጽ የሚሰጡ ቁርጥራጭ ነገሮችን ማለት ነው።

• ሻኵራንና ሮማንን፥ ሻኵራንና ሮማንን ለማገልገል አደረጉ

በአገልግሎት ወቅት እንዲለብሱ ጸናጽሎችንና ሮማን ፍሬ መሳይ ስዕሎችን በቀሚሱ ጠርዝ ወይም ጫፍ ዙሪያ አደረጉ

Exodus 39:27

አጠቃላይ ምልከታ፦

በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው … አደረጉ

እንደነዚህ ያሉትን ክፍሎች በ28፡39-40 እና 42 ላይ ያለውን እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት።

• መጠምጠሚያ

ወንዶች ራሳቸውን የሚሸፍኑበት ከጨርቅ የተሰራ ራስ ጥምጥም

• የእግር ሱሪዎችን

ከሌሎች ልብሶች ቀደም ተብሎ የሚለበስ የውስጥ ሱሪ ማለት ነው፥ (የጋራ መረዳትና ያልተገለጹ ሀሳቦች እንዴት እንተረጉማለን የሚለውን ተመልከት)

• መታጠቂያ

በትከሻ ወይም አንገትጌ ላይ የሚለበስና እንዲሁም በወገብ ላይ የሚለበስ የወገብ መታጠቂያ ነው።

Exodus 39:30

አጠቃላይ ምልከታ፦

በምዕራፍ 28፡36-37 ላይ በተሰጠው መመሪያ መሰረት በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ካህናት ልብሶች ዝግጅት ይቀጥላል

• የተቀደሰ የአክሊል

ከንጹህ ወርቅ በራስ ላይ የሚደረግ ቆብ መሳይ ነገር

Exodus 39:32

አጠቃላይ ምልከታ፦

በምዕራፍ 35፡4-9 እና 35፡10-12 ላይ በተሰጠው መመሪያ መሰረት እስራኤላውያን የተሰጣቸውን ሥራ ሲጨርሱ ያሳየናል።

• እንዲሁም የመገናኛው ድንኳን የማደሪያውም ሥራ ሁሉ ተጨረሰ

ይህ በተደራጊ ግስ የተገለጸው ዐረፍተ ነገር “የእስራኤል ልጆች የመገናኛውን ድንኳን ሥራውን ሁሉ ጨረሱ” በሚለው ልተረጎም ይችላል። “የመገናኛው ድንኳን የማደሪያውም” የሚሉ ቃላት ሁለቱም ስለአንድ ነገር የሚያወሩ ናቸው።

• የማደሪያውን ድንኳን ወደ ሙሴ አመጡት

የእስራኤል ሰዎች እግዚአብሔር ሙሴን ባዘዘው መሰረት የተሰራውን የመገናኛውን ድንኳን ወደ ሙሴ አመጡ ማለት ነው።

• መያዣዎች

መጋረጃዎችን በአንድ ለማያያዝ የሚጠቅሙ ነገሮች ወይም አቃፊዎች ናቸው። ዘጸአት 26፡4-6 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት።

• እግሮቹንም

ምሶሶዎች የሚቆሙባቸው እግሮች ማለት ነው።

• የስርየት መክደኛውንም

ከታቦቱ ላይ የሚቀመጥ መሸፈፍኛ ወይም መክደኛ ሲሆን የስርየት መስዋዕት የሚቀርብበትም ጭምር ነው።

Exodus 39:36

አጠቃላይ ምልከታ፦

በባስልኤልና በሥሩ ያሉ የሥራ ቡድኖች ማደሪያውንና መገናኛ ድንኳኑን ለሙሴ ሲያቀርቡ እናያለን።

• የገጹንም ኅብስት

ህልዎተ እግዚአብሔር መገለጫ የሆነው ዳቦ ነው። በመገናኛው ድንኳን ወይም በማደሪያው ውስጥ የእግዚአብሔር መኖር ምልክት የሆነው ዳቦ ነው። ከተራ ዳቦ የተለየ መሆኑን ለማመልከት በአማርኛ ኅብስት ተብሏል። ዘጸአት 25፡30 ተመልከት

• ከናስ መጫሪያው

እንጨት በእሳት ሲነድ በአንድ በኩል እንጨቱን ለመያዝ የሚያገለግል ከነሐስ ብረት የተሰራ ዘንግ ማለት ነው።

Exodus 39:40

አጠቃላይ ምልከታ፦

በባስልኤልና በሥሩ ያሉ የሥራ ቡድኖች ማደሪያውንና መገናኛ ድንኳኑን ለሙሴ ሲያቀርቡ እናያለን።

• የእስራኤል ልጆች ሥራውን ሁሉ ሠሩ

ሥራውን በሀላፊነት የሚመራው ባስልኤልና የእርሱ ቡድን ይሁን እንጂ እስራኤላውያንም በሥራው ላይ ተሳታፊ ነበሩ።

• እነሆም አድርገውት ነበር

በትክክልና በታዘዙት መሰረት ሰርተውት ነበር።


Chapter 40

1 ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ 2 “በዐዲሱ ዓመት የመጀመሪያ ወር የመጀመሪያ ቀን ማደረያውን፣ የመገናኛውን ድንኳን ትከለው። 3 ታቦት በውስጡ አስቀምጠው፤ ታቦቱንም በመጋረጃ ከልለው። 4 ጠረጴዛውንም ወደ ውስጥ አምጣና በላዩ የሚቀመጡትን ዕቃዎች በሥርዐት አስቀምጥ። ከዚያም መቅረዙን አስገብተህ መብራቶቹን አስተካክል። 5 የወርቅ የዕጣን መሠዊያውን በምስክሩ ታቦት ፊት አስቀምጥ፤ የመገናኛውን ድንኳን መግቢያ መጋረጃም አድርግ። 6 የሚቃጠሉ መሥዋዕቶችን መሠዊያ በማደሪያው፣ በመገናኛው ድንኳን ፊት ለፊት አስቀምጥ። 7 ትልቁን የመታጠቢያ ሳሕን በመገናኛው ድንኳንና በመሠዊያው መካከል አስቀምጠው፤ ውሀም አድርግበት። 8 በዙሪያውም አደባባይ ሥራለትን በአደባባዩ መግቢያ ላይ መጋረጃውን ስቀል። 9 መቅቢያ ዘይቱን ውሰድና መገናኛውን ድንኳንና አውስጡ ያለውን ዕቃ ሁሉ ቅባ። እርሱንና በውስጡ ያለውን ዕቃ ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ፤ ከዚያም የተቀደሰ ይሆናል። 10 የሚቃጠሉ መሥዋዕቶችን መሠዊያና የመሠዊያውን ዕቃዎች ሁሉ ቅባቸው። 11 መሠዊያውን ለእኔ ቀድስልኝ፤ ከዚያም ለእኔ እጅግ የተቀደሰ ይሆንልኛል። 12 ልጆቹን ወደ መገናኛው ድንኳን መግቢያ አምጣና በውሀ እጠባቸው። 13 ለእኔ የተቀደሱ ልብሶችን ለአሮን አልብሰው፤ ካህኔ ሆኖ እንዲያገለግልም ቅባው፤ ቀድሰውም። 14 ልጆቹንም አምጣና ሸሚዞችን አልብሳቸው። 15 ካህናቴ ሆነው እንዲያገለግሉኝ፣ አባታቸውን እንደ ቀባኸው እነርሱንም ቅጣቸው። የእነርሱ መቀባት በትውልዶች ሁሉ የዘለቄታ ካህንነትን ለእነርሱ ያስገኛል።” 16 ሙሴ ያደረገው ይህ ነው፦ እግዚአብሔር ያዘዘውን ሁሉ ተከተለ። እነዚህንም ሁሉ አደረገ። 17 በሁለተኛው ዓመት የመጀመሪያ ወር አንደኛ ቀን ላይ የመገናኛው ድንኳን ተተከለ። 18 ሙሴ መገናኛውን ድንኳን ተከለ፤ መቆሚያዎቹንም በስፍራቸው አስቀመጠ፤ ወጋግራዎቹን አቁሞ አግዳሚዎቹን አያያዘ፤ ምሰሶዎቹንም አቆመ። 19 በማደሪያው ላይ መሸፈኛውን ዘረጋ፤ ድንኳኑንም እግዚአብሔር አዝዞት እንደ ነበረው ከበላዩ አስቀመጠው። 20 ምስክሩን ወስዶ በታቦቱ ውስጥ አስቀመጠው። 21 ወደ መገናኛው ድንኳን አመጣው። እግዚአብሔር ሙሴን አዝዞት እንደ ነበረው፣ የምስክሩን ታቦት ለመከለል መጋረጃውን አደረገ። 22 ሰሜን ጎን ከመጋረጃው ውጭ ጠረጴዛውን በመገናኛው ድንኳን ውስጥ አስቀመጠ። 23 እግዚአብሔር አዝዞት እንደ ነበረው፣ ኅብስቱን በጠረጴዛው ላይ በሥርዐት በእግዚአብሔር ፊት አስቀመጠው። 24 መቅረዙን በመገናኛው ድንኳን ደቡብ ጎን ከጠረጴዛው ትይዩ በማደሪያው ድንኳን ውስጥ አስቀመጠው። 25 መብራቶቹን እግዚአብሔር እንዳዘዘው በእግዚአብሔር ፊት አበራቸው። 26 የተሠራውን የዕጣን መሠዊያም በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ከመጋረጃው ፊት ለፊት አደረገው። 27 ላይም እግዚአብሔር አዝዞት እንደ ነበረው ጣፋጭ መዐዛ ያለውን ዕጣን አቀጣጠለ። 28 መጋረጃውን በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ ሰቀለ። 29 የሚቃጠለውን መሥዋዕት መሠዊያም በማደሪያው፣ በመገናኛው ድንኳን መግቢያ አስቀመጠ። በመሠዊያውም ላይ የሚቃጠለውን መሥዋዕትና የእህሉን ቍርባን እግዚአብሔር እንዳዘዘው አቀረበ። 30 የመታጠቢያ ሳሕኑን በመገናኛው ድንኳንና በመሠውያው መካከል አኖረው፤ የመታጠቢያ ውሀም በውስጡ አደረገ። 31 ሙሴ፣ አሮንና ልጆቹ እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን በመታጠቢያው ውሀ ይታጠቡ ነበር፤ 32 መገናኛው ድንኳን ውስጥ በሚገቡትና መሠዊያው ወዳለበት ወደ ላይ በሚወጡበት ጊዜ ሁሉ፣ እግዚአብሔር ሙሴን ባዘዘው መሠረት ታጥበውታል። 33 ሙሴ በመገናኛው ድንኳንና በመሠዊያው ዙሪያ አደባባዩን አቆመ። መጋረጃውንም በአደባባዩ መግቢያ ዘረጋ። ሙሴ በዚህ መንገድ ሥራውን ፈጸመ። 34 ደመናውም የመገናኛውን ድንኳን ሸፈነ፤ የእግዚአብሔር ክብርም ማደሪያውን ሞላው። 35 ደመናው በላዩ ስላረፈና የእግዚአብሔር ክብርም ማደሪያውን ስለ ሞላው፣ ሙሴ መገናኛው ድንኳን ውስጥ መግባት አልቻለም ነበር። 36 ከማደሪያው ድንኳን በተነሣ ጊዜ ሁሉ፣ የእስራኤል ሰዎች ይጓዛሉ። 37 ግን ደመናው ከማደሪያው ላይ ካልተነሣ፣ ሕዝቡ አይጓዙም። ደመናው እስከሚነሣበት ቀን ድረስ ይቆያሉ። 38 በሁሉም የእስራኤል ሕዝብ ፊት በጕዟቸው ሁሉ ቀን የእግዚአብሔር ደመና፣ ማታ ደግሞ እሳቱ በማደሪያው ላይ ነበረ።



Exodus 40:1

• ከመጀመሪያው ወር በፊተኛው ቀን

እስራኤላውያን ከግብጽ የወጡበት ቀን የዓመቱ የመጀመሪያ ወር ሆኖ ተቆጠረላቸው። ይህ ወር ለእስራኤላውያን ሚያዚያ ወር ነው። የመጽሐፍ ቅዱሱ የወር አቆጠጠር የሚጀምረው በዚሁ ወር ነው።

Exodus 40:3

• በእርሱም ውስጥ የምስክሩን ታቦት ታኖራለህ

በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የምስክሩን ወይም የቃል ኪዳኑን ታቦት ታኖራለህ

• ታቦቱንም በመጋረጃ ትጋርዳለህ

ታቦቱን ከመጋረጃው በስተጀርባ ወይም ታቦቱን በመጋረጃ ትጋርዳለህ ማለት ነው

Exodus 40:5

• የምስክር ታቦት

በሌላ ስሙ የሚታወቀው የቃል ኪዳን ታቦት ተብሎ ነው። በድንጋይ ጽላት ላይ የተጻፉት ቃላት እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ለገባው ቃል ኪዳን ምስክር እንዲሆን ነው።

Exodus 40:8

• የቅብዓት ዘይት

ይህ የወይራ ዘይት ሲሆን ማደሪያ ድንኳኑንና ሌሎችንም ዕቃዎች ለእግዚአብሔር የተለየ ለማድረግ ወይም ቅዱስ ለማድረግ የሚቀቡት ነው።

Exodus 40:12

• ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ አቅርበህ

ሙሴ አሮንና ልጆቹን ወደ መገናኛው ድንኳን እንዲያመጣቸው ትእዛዝ ተሰጠው።

• በክህነትም ያገለግለኝ ዘንድ ቀብተህ ትቀድሰዋለህ

አሮንን ለእኔ የተለየ ካህን ሆኖ እንዲያገለግለኝ አድርገው

Exodus 40:14

• ለልጅ ልጃቸው ለዘላለም ክህነት ይሆንላቸዋል

በሚመጡት ዘመናት ወይም ትውልዶች ሁሉ ካህናት ሆነው ያገለግሉኛል

Exodus 40:17

• ማደሪያው ተተከለ

ሙሴ መገናኛውን ደንኳን ወይም ማደሪያውን ድንኳን ተከለ በሚል በአድራጊ ግስ መተርጎም ይቻላል።

• በሁለተኛው ዓመት በፊተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን

ይህ የነገናኛው ድንኳን ተከላና አሰራር የተፈጸመው ልክ እስራኤላውያን ከግብጽ በወጡ በሁለተኛው ዓመት በሁለተኛው ወር በወሩም በመጀመሪያው ቀን ላይ ነበር።

• እግዚአብሔርም እንዳዘዘው ሙሴ ማደሪያውን ተከለ

ሙሴ የድንኳኑን ተከላ የሚመራ መሪ ይሁን እንጂ ህዝቡ ያግዙትና በሥራው ይተባበሩት ነበር።

• ወጋግራዎቹን አቆመ

እግሮቹንም አኖረ ወይም ምሰሶዎቹን አቆመ የሚል ነው።

Exodus 40:21

• ታቦቱን ወደ ማደሪያው አገባ

ታቦቱን ወደ መገናኛው ድንኳን ውስጥ አስገባው ወይም አስገብቶ አስቀመጠ የሚል ይሆናል

Exodus 40:24

• ቀንዲሎቹን በእግዚአብሔር ፊት ለኰሰ

በእግዚአብሔር ፊት መብራቶቹን አበራ

Exodus 40:26

• በመጋረጃው ፊት አኖረ

ይህ መጋረጃ ቅድስተ ቅዱሳንን ከቅዱስ ስፍራው የሚለየው ነው። ስለሆነም የወርቁን መሰዋያዊ ከመጋረጃው ፊት ለፊት ሲያስቀምጥ ቅድስተ ቅዱሳኑ ከበስተሁዋላው ነው ማለት ነው።

Exodus 40:28

• በእርሱም ሙሴና አሮን ልጆቹም እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ታጠቡ

በመታጠቢያው ሳህን ባለው ውሃ ውስጥ አሮንና ልጆቹ እጆቻቸውንና እግራቸውን ታጠበ።

Exodus 40:31

• በእርሱም ሙሴና አሮን ልጆቹም እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ታጠቡ

በመታጠቢያው ሳህን ባለው ውሃ ውስጥ አሮንና ልጆቹ እጆቻቸውንና እግራቸውን ታጠበ።

Exodus 40:34

• የእግዚአብሔርም ክብር ማደሪያውን ሞላ

የእግዚአብሔርም መገኘት የመገናኛ በድንኳኑ ውስጥ ይታይ ነበር።

Exodus 40:36

• ደመናውም ከማደሪያው በተነሣ ጊዜ

በጉዞአቸው ሁሉ እስራኤላውያን የሰፈሩበትን ቦታ ለቀው የሚንቀሳቀሱት ደመናው ከድንኳኑ ላይ በሚነሣበት ጊዜ ብቻ ነበር።


Book: Leviticus


Leviticus

Chapter 1

1 ያህዌ ከመገናኛው ድንኳን ሆኖ ሙሴን ጠርቶ እንዲህ አለው፣ 2 “ለእስራኤላዊያን እንዲህ ብለህ ንገራቸው፣ ‘ከእናንተ መሃል ማንም ሰው ለያህዌ መባ በሚያቀርብበት ጊዜ ከከብቶቻችሁ ወይም ከመንጋው እንስሳት መሃል አንዱን ያቅርብ፡፡ 3 መባው ከመንጋው መሃል የሚቃጠል መስዋዕት ከሆነ፣ ነውር የሌለበት ወንድ መስዋዕት ያቅርብ፡፡ መስዋዕቱ በያህዌ ፊት ተቀባይነት ያለው ይሆን ዘንድ በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ያቅርበው፡፡ 4 በሚቃጠለው መስዋዕት ራስ ላይ እጁን ይጭናል፣ ይህም በእርሱ ምነትክ ያስተሰርይለት ዘንድ ተቀባይነት ያገኛል፡፡ 5 ከዚያ በያህዌ ፊት ወይፈኑን ይረድ፡፡ በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ካህናቱ የአሮን ልጆች ደሙን ያቀርቡና በመሰዊያው ላይ ይረጩታል፡፡ 6 ከዚያም ካህኑ የመስዋዕቱን ከብት ቆዳ መግፈፍና ብልቶችንም ማውጣት ይኖርበታል፡፡ 7 ከዚያም ካህናቱ የአሮን ልጆች በመሰዊያው ላይ ዕሳት ይለኩሱና እንጨት ይጨምሩበታል፡፡ 8 ካህናቱ የአሮን ልጆች የስጋውን ብልቶች፣ የከብቱን ጭንቅላትና ስቡን በመስዋዕቱ ምድጃ ላይ በሚገኘው እንጨት ላይ በስርዓት ይደረድሩታል፡፡ 9 ነገር ግን ካህኑ የመስዋዕቱን ሆድቃና እግሮቹን በውሃ ማጠብ ይኖርበታል፡፡ በመስዋዕቱ ላይ የሚገኘውን ሁሉ የሚቃጠል መስዋዕት አብርጎ ያቃጥለዋል፡፡ ይህም ለእኔ ጣፋጭ ሽታ ይሆናል፤ ይህም ለእኔ በዕሳት የቀረበ መስዋዕት ይሆናል፡፡ 10 ለመስዋዕት የሚያቀርበው የሚቃጠል መስዋዕት ከመንጋው ከሆነ፣ ከበጎች ወይም ከፍየሎች መሃል ነውር የሌለበት ተባዕት መስዋዕት ማቅረብ አለበት፡፡ 11 በያህዌ ፊት መስዋዕቱን ከመሰዊያው በስተቀኝ በኩል ይረደው፡፡ ካህናቱ የአሮን ልጆች የመስዋዕቱን ከብት ደም በመሰዊያው ዙሪያ ሁሉ ይርጩት፡፡ 12 ከዚያ ካህኑ የመስዋዕቱን ከብት ጭንቅላቱንና ስቡን እንዲሁም ብልቶቹን ይቆራርጥ፡፡ ከዚያም በመሰዊያው በሚገኘው የሚነድ እንጨት ላይ በስርዓት ይደርድረው፡፡ 13 ነገር ግን የመስዋዕቱን ሆድቃና እግሮቹን በውሃ ይጠብ፡፡ ከዚያ ካህኑ መባውን በሙሉ ያቅርብና በመሰዊያው ላይ ያቃጥለው፡፡ ይህም የሚቃጠል መስዋዕት ነው፣ ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ ይሆናል፤ ለእርሱ በዕሳት የተዘጋጀ መስዋዕት ይሆናል፡፡ 14 “ካህኑ ለያህዌ የሚያቀርበው የሚቃጠል የወፎች መስዋዕት ከሆነ፣አንድ ወፍ ወይም ዕርግብ ማቅረብ አለበት፡፡ 15 ካህኑ መስዋዕቱን ወደ መሰዊያው ያመጣና አንገቱን ይቆለምመዋል፣ ከዚያም በመሰዊያው ላይ ያቃጥለዋል፡፡ ደሙም በመሰዊያው ጎን ተንጠፍጥፎ ይፈሳል፡፡ 16 የወፉን ማንቁርትና በውስጡ ያሉትን ያስወግድ፣ ከዚያም አመድ በሚደፉበት ከመሰዊያው በስተ ምስራቅ ይወርውረው፡፡ 17 ክንፎቹን ይዞ ይሰንጥቀው፣ ነገር ግን ለሁለት አይክፈለው፡፡ ከዚያ ካህኑ በዕሳቱ ላይ ባለው እንጨት መሰዊያው ላይ ያቃጥለው፡፡ ይህ የሚቃጠል መስዋዕት ይሆናል፣ እናም ለያህዌ ጣፋጭ ማዕዛ ይሆናል፣ ይህ ለእርሱ በዕሳት የተዘጋጀ መስዋዕት ይሆናል፡፡”



Chapter 2

1 ማንኛውም ሰው ለያህዌ የእህል ቁርባን ሲያቀርብ፣ መባው መልካም ዱቄት ይሁን፣ ዘይት ያፈስበታል ደግሞም ዕጣን ያድርግበት፡፡ 2 ቁርባኑን ወደ ካህናቱ ወደ አሮን ልጆች ይወስደዋል፣ ካህኑ ከዘይቱና በላዩ ካለው ዕጣን ጋር ከመልካሙ ዱቄት እፍኝ ይወስዳል፡፡ ከዚየም ካህኑ የያህዌን በጎነት ለማሰብ መስዋዕቱን በመሰዊያው ላይ ያቃጥለዋል፡፡ ይህም ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ ነው፣ ለእርሱ በዕሳት የቀረበ መስዋዕት ይሆናል፡፡ 3 ከእህል መስዋዕቱ የተረፈው ሁሉ ለአሮንና ለልጆቹ ይሆናል፡፡ ይህ ሙሉ ለሙሉ ለያህዌ በዕሳት ከተዘጋጀው መስዋዕት ለእርሱ የተለየ ነው፡፡ 4 በምድጃ የተጋገረ እርሾ የሌለበት የእህል ቁርባን ስታቀርብ፣ በዘይት የተለወሰ ከመልካም ዱቄት የተዘጋጀ ለስላሳ ዳቦ መሆን አለበት፣ ወይም እርሾ የሌለበት በዘይት የተቀባ ቂጣ መሆን አለበት፡፡ 5 የእህል ቁርባንህ በመጥበሻ ላይ የተጋገረ ከሆነ፣ እርሾ ያልገባበት በዘይት የተለወሰ ከመልካም ዱቄት የተዘጋጀ ይሁን፡፡ 6 ቆራርሰህ በላዩ ዘይት ጨምርበት፡፡ ይህ የእህል ቁርባን ነው፡፡ 7 የእህል ቁርባንህ በመጥበሻ የሚዘጋጅ ከሆነ ከመለካም ዱቄትና ዘይት ይዘጋጅ፡፡ 8 ከእነዚህ ነገሮች የተዘጋጀውን የእህል ቁርባን ወደ ያህዌ ማቅረብ አለብህ፣ እናም ይህ ወደ መሰዊያው ወደሚያመጣው ወደ ካህኑ ይቅረብ፡፡ 9 ከዚያም የያህዌን በጎነት ለማሰብ ካህኑ ከእህል ቁርባኑ ጥቂት ይወስዳል፣ ቀጥሎም በመሰዊያው ላይ ያቃጥለዋል፡፡ ይህ በዕሳት የተዘጋጀ መስዋዕት ይሆናል፣ እናም ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ ይሆናል፡፡ 10 ከእህል ቁርባኑ የሚተርፈው ለአሮንና ለልጆቹ ይሆናል፡፡ ይህ ለያህዌ በዕሳት ከሚዘጋጀው ቁርባን ሙሉ ለሙሉ ለእርሱ የተለየ ነው፡፡ 11 ለያህዌ በምታቀርቡት የእህል ቁርባን ውስጥ እርሾ አይግባበት፣ ለያህዌ በዕሳት በምታዘጋጁት ቁርባን ውስጥ ምንም እርሾ፣ ወይም ማር አታቃጥሉ፡፡ 12 እነዚህን እንደ በኩራት ፍሬዎች ለያህዌ ታቀርባላችሁ፣ ነገር ግን በመሰዊያው ላይ መልካም መዓዛ ለመስጠት አታቀርቧቸውም፡፡ 13 የእህል ቁርባንህን ሁሉ በጨው አጣፍጠው፡፡ ከእህል ቁርባንህ በፍጽም የአምላክህ የቃል ኪዳን ጨው አይታጣ፡፡ በመስዋዕቶችህ ሁሉ ጨው ማቅረብ አለብህ፡፡ 14 ለያህዌ ከፍሬህ በኩራት የእህል ቁርባን ስታቀርብ ከእሸቱ በእሳት የተጠበሰውንና የተፈተገውን አቅርብ፡፡ 15 ከዚያ በላዩ ላይ ዘይትና እጣን ጨምርበት፡፡ ይህ የእህል ቁርባን ነው፡፡ 16 ከዚያ ካህኑ የተፈተገውን እህል እና ዘይት እንዲሁም ዕጣን የያህዌን በጎነት በአንክሮ ለማሰብ ከፊሉን ያቃጥለዋል፡፡ ይህም ለያህዌ የሚቀርብ የዕሳት መስዋዕት ነው፡፡



Chapter 3

1 ማንኛውም ሰው ከመንጋው መሃል ወንድም ሆነ ሴት እንስሳ የህብረት መስዋዕት እንስሳ ቢያቀርብ፣በያህዌ ፊት ነውር የሌለበት እንስሳ ያቅርብ፡፡ 2 እጁን በመስዋዕቱ እንስሳ ራስ ላይ ይጭናል፣ ከዚያም በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ ያርደዋል፡፡ ከዚያ ካህናቱ የአሮን ልጆች በመሰዊያው ዙሪያ ደሙን ይረጩታል፡፡ 3 የህብረት መስዋዕቱን ለያህዌ በዕሳት ያቀርባል፡፡ ሆድቃውን የሸፈነውን ወይም ከዚያ ጋር የተያያዘውን ስብ፣ 4 እና ሁለቱን ኩላሊቶች እንዲሁም በጎድኑ አጠገብ የሚገኘውን ስብ፣ እና የጉበቱን መረብ ከኩላሊቶቹ ጋር እነዚህን ሁሉ አውጥቶ ያቀርባል፡፡ 5 የአሮን ልጆች ከሚቃጠለው መስዋዕት ጋር እነዚህን በዕሳቱ ላይ በሚገኘው እንጨት በመሰዊያው ላይ ያቃጥሉታል፡፡ ይህም ለያህዌ ጣፋጭ ማዕዛ ይሆናል፣ ይህ በእሳት ለያህዌ የሚቀርብ መስዋዕት ይሆናል፡፡ 6 ለያህዌ የሚያቀርበው የህብረት መስዋዕት ወንድም ይሁን ሴት እንስሳ ነውር የሌለበት ይሁን፡፡ 7 መስዋዕቱ የበግ ጠቦት ከሆነ፣ በያህዌ ፊት ያቅርበው፡፡ 8 እጁን በመስዋዕቱ ራስ ላይ ይጫንና በመገናኛው ድንኳን ፊት ለፊት ይረደው፡፡ ከዚያ አሮን ልጆች በመሰዊያው ጎንና ጎኖች ደሙን ይረጩታል፡፡ 9 የህብረት መስዋዕቱን በእሳት እንደሚቀርብ መስዋዕት አድርጎ ለያህዌ ያቀርባል፡፡ ስቡን፣ላቱን እስከ ጀርባ አጥንቱ ድረስ፣እንዲሁም የሆድ እቃውን የሸፈነውን ስብ ሁሉ፣በሆድ እቃው ዙሪያ የሚገኘውን ስብ ሁሉ፣ 10 እና ሁለቱን ኩላሊቶችና ከእነዚህ ጋር ያለውን ስብ፣ በጎድኑ አጠገብ የሚገኘውን እና የጉበቱን መሸፈኛ ከኩላሊቶቹ ጋር እነዚህን ሁሉ አውጥቶ ያቀርባል፡፡ 11 ከዚያም ካህኑ ሁሉንም ለያህዌ በመሰዊያው ላይ በእሳት የመበል ቁርባን አድርጎ ያቃጥላል፡፡ 12 የሚያቀርበው መስዋዕት ፍየል ከሆነ፣በያህዌ ፊት ያቅርበው፡፡ 13 እጁን በፍየሉ ራስ ላይ መጫንና በመገናኛው ድንኳን ፊት ለፊት ማረድ ይኖርበታል፡፡ ከዚያ አሮን ልጆች በመሰዊያው ጎንና ጎኖች ደሙን ይረጩታል፡፡ 14 በእሳት የተዘጋጀውን መስዋእቱን ለያህዌ ያቀርባል፡፡ የሆድ እቃውን የሸፈነውንና በሆድ እቃው ዙሪያ የሚገኘውን ስብ ሁሉ አውጥቶ ያቀርባል፡፡ 15 እንዲሁም ሁለቱን ኩላሊቶችና ከእነዚህ ጋር የሚገኘውን ስብ፣ በጎድኖች እና ከኩላሊቶቹ ጋር በጉበቱን መሸፈኛው ላይ የሚገኘውን ስብ እነዚህን ሁሉ አውጥቶ ያቀርባል፡፡ 16 ካህኑ እነዚህን ሁሉ በመሰዊያው ላይ መልካም መዓዛ እንዲሆን እንደ መብል መስዋዕት አድርጎ ሁሉንም ያቃጥለዋል፡፡ ስቡ ሁሉ የያህዌ ነው፡፡ 17 “‘ይህ ለእናንተ ከትውልድ እስከ ትውልድ በምትኖሩበት ስፍራ ሁሉ ቀዋሚ መታሰቢያ ነው፣ እናንተ ስብ ወይም ደም አትብሉ፡፡’”



Chapter 4

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 2 “ለእስራኤል ህዝብ እንዲህ ብለህ ንገራቸው፣ ‘ማንም ሰው ያህዌ እንዳይደረግ ያዘዘውን ማናቸውንም ነገር በማድረግ ኃጢአት መስራት ሳይፈልግ ኃጢአት ቢሰራ፣ ደግሞም የተከለከለ አንዳች ነገር ቢያደርግ፣ እንዲህ ይደረግ፡፡ 3 ኃጢአት የሰራው ሊቀ ካህኑ ቢሆንና በህዝቡ ላይ በደል የሚያስከትል ኃጢአት ቢሰራ ስለ ሰራው ኃጢአት ለያህዌ ነውር የሌለበት ወይፈን የኃጢአት መስዋእት አድርጎ ያቅርብ፡፡ 4 ወይፈኑን በያህዌ ፊት ወደ መገናኛው ድንኳን ያምጣ፤ ካህኑ እጆቹን በወይፈኑ ራስ ላይ ይጫንና በያህዌ ፊት ይረደው፡፡ 5 የተቀባው ካህን ከወይፈኑ ጥቂት ደም ይውድና ወደ መገናኛው ድንኳን ያምጣው፡፡ 6 ካህኑ ጣቱን ደሙ ውስጥ እየነከረ ሰባት ጊዜ በቅድስተ ቅዱሳኑ መጋረጃ ላይ ከደሙ ጥቂት በያህዌ ፊት ይረጫል፡፡ 7 ደግሞም ካህኑ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በያህዌ ፊት ከደሙ ጥቂት ወስዶ መልካም መዓዛ ያለውን ዕጣን በመሰዊያው ቀንዶች ይጨምራል፤ የቀረውን ወይፈኑን ደም ሁሉ በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ ለሚቃጠል መስዋዕት በመሰዊያው ስር ያፈሰዋል፡፡ 8 የሆድ ዕቃውን የሸፈነውንና ከሆድ ዕቃው ጋር የተያያዘውን የበደል መስዋዕቱን የሆነውን ወይፈን ስብ ሁሉ አውጥቶ ያቀርባል፡፡ 9 (ቁጥር 9?) 10 ለህብረት መስዋዕት ከሚቀርበው ወይፈን አውጥቶ እንዳቀረበ ሁሉ ይንንም አውጥቶ ያቀርባል፡፡ ከዚያም ካህኑ እነዚህን ክፍሎች ለሚቃጠል መስዋዕት በመሰዊያው ላይ ያቃጥላል፡፡ 11 የወይፈኑን ቆዳና ማንኛውንም ስጋ ከጭንቅላቱና ከእግሮቹ እንዲሁም ከሆድዕቃው ክፍሎችና ከፈርሱ ጋር፣ 12 የቀረውን የወይፈኑን ክፍሎች ሁሉ ከእነዚህ ክፍሎች ሁሉ ከመንደር ተሸክሞ አመዱን ወደ ደፉበት ለእኔ ወደሚነጹበት ስፍራ ወስዶ እነዚያን ክፍሎች በእንጨት ላይ ያቃጥላቸው፡፡ እነዚያን የከብቱን ክፍሎች አመዱን በደፉበት ስፍራ ያቃጥለው፡፡ 13 መላው የእስራኤል ጉባኤ ኃጢአት መስራት ሳይፈልግ ኃጢአት ቢሰራ፣ ጉባኤውም ኃጢአት መስራቱን ባያውቅና ያህዌ እንዳይደረግ ያዘዘውን ማናቸውንም ነገር ፈጽሞ ቢገኝና በደለኛ ቢሆን፣ 14 ከዚያም፣ የፈጸሙት በደል በታወቀ ጊዜ፣ ጉባኤው ለኃጢአት መስዋዕት ወይፈን ይሰዋና ወደ መገናኛው ድንኳን ፊት ያምጣው፡፡ 15 የጉባኤው ሽማግሌዎች በያህዌ ፊት በወይፈኑ ላይ እጃቸውን ይጫኑና በያህዌ ፊት ይረዱት፡፡ 16 የተቀባው ካህን ከወይፈኑ ደም ወደ መገናኛው ድንኳን ያመጣል፣ 17 ከዚያ ካህኑ ጣቱን በደሙ ውስጥ ነክሮ በመጋረጃው ላይ በያህዌ ፊት ሰባት ጊዜ ይረጨዋል፡፡ 18 በመገናኛው ድንኳን ውስጥ፣በያህዌ ፊት በመሰዊያው ቀንዶች ውስጥ ከደሙ ጥቂት ይጨምርበታል፤ ደግሞም ለሚቃጠል መስዋዕት በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ በመሰዊያው ታች ደሙን በሙሉ ያፈሳል፡፡ 19 ስቡን ሁሉ ከእንስሳው ቆርጦ ያወጣና በመሰዊያው ላይ ያቃጥላል፡፡ 20 ወይፈኑን በዚህ መልክ ለመስዋዕት ያቀርባል፡፡ ለኃጢአት መስዋዕት እንዳቀረበው ወይፈን ሁሉ፣ በዚህኛውም ወይፈን ይህንኑ ያደርጋል፣ እናም ካህኑ ለህዝቡ ማስተስረያ ያደርጋል፣ እናም ጉባኤው ይቅር ይባላል፡፡ 21 ካህኑ ወይፈኑን ከመንደር ያወጣና የመጀመሪያውን ወይፈን እንዳቃጠለ ይህኛውንም ያቃጥለዋል፡፡ ይህ ለጉባኤው የኃጢአት መስዋዕት ነው፡፡ 22 የህዝቡ መሪ ኃጢአት ለመስራት ሳያስብ ኃጢአት ቢሰራ፣ አምላኩ ያህዌ እንዳይደረግ ካዘዘው ማናቸውም ነገሮች አንዱን አድርጎ ቢገኝና በደለኛ ቢሆን፣ 23 ከዚያም የሰራው ኃጢአት ቢታወቀው፣ ነውር የሌለበት ተባዕት ፍየል ለመስዋዕት ያቀርባል፡፡ 24 እጁን በፍየሉ ራስ ላይ ይጭንና የሚቃጠል መስዋዕት በሚያርዱበት ስፍራ በያህዌ ፊት ይረደው፡፡ ይህ የኃጢአት መስዋዕት ነው፡፡ 25 ካህኑ ያኃጢአት መስዋዕቱን ደም በጣቱ ይውሰድና ለሚቃጠል መስዋዕት በመሰዊያው ቀንዶች ውስጥ ይጨምረው፣ ደግሞም ደሙን ለሚቃጠል መስዋዕት በመሰዊያው ስር ያፍስሰው፡፡ 26 ልክ እንደ ሰላም መስዋዕት ሁሉ ስቡን በሙሉ በመሰዊያው ላይ ያቃጥለው፡፡ ካህኑ የህዝቡ መሪ ለሰራው ኃጢአት ማስተስረያ ያድርግለታል፣ መሪውም ይቅር ይባላል፡፡ 27 ከተራው ህዝብ መሃል አንድ ሰው ኃጢአት ለማድረግ ሳያስብ ኃጢአት ቢሰራ፣ያህዌ እንዳይደረግ ካዘዘው ከእነዚህ ነገሮች መሃል አንዱን ቢፈጽም፣ እናም በደለኛ ሆኖ ቢገኝ፣ 28 ከዚያም የፈጸመው በደል ቢታወቀው፣ ለበደሉ መስዋዕት ነውር የሌለበት ሴት ፍየል ያቅርብ፡፡ 29 በኃጢአት መስዋዕቱ ራስ ላይ እጁን ይጭናል ከዚያም በሚቃጠል መስዋዕቱ ስፍራ የኃጢአት መስዋዕቱን ያርዳል፡፡ 30 ካህኑ በጣቱ ጥቂት ደም ወስዶ ለሚቃጠል መስዋዕት በመሰዊያው ቀንዶች ውስጥ ይጨምረዋል፡፡ የተቀረውን ደም ሁሉ በመሰዊያው ስር ያፈሰዋል፡፡ 31 መስዋዕቱ በተወሰደበት ሁኔታ ከዚህኛውም ሁሉንም ስብ ይወስዳል፡፡ ካህኑ ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ ለማቅረብ በመሰዊያው ላይ ያቃጥለዋል፣የሰውየውንም ኃጢአት ያስተሰርያል፡፡ 32 ለኃጢአት መስዋዕቱ የበግ ጠቦት ቢያቀርብ ነውር የሌለባት ሴት ጠቦት ያምጣ፡፡ 33 በኃጢአት መስዋዕቱ ራስ ላይ እጁን ይጫንና የሚቃጠል መስዋዕት በሚያርድበት ስፍራ ለኃጢአት መስዋዕት ያርዳል፡፡ 34 ካህኑ ከኃጢአት መስዋዕቱ ጥቂት ደም ይወስድና ለሚቃጠል መስዋዕት በመሰዊያው ቀንዶች ውስጥ ይጨምረዋል፡፡ ከዚያም በመሰዊያው ስር ደሙን ሁሉ ያፈሰዋል፡፡ 35 ከሰላም መስዋዕቱ የጠቦቱ ስብ በወጣበት ሁኔታ፣ከዚህኛውም ሁሉንም ስብ ይወስዳል፣ከዚያ ካህኑ በያህዌ መስዋዕቶች ላይ በእሳት በሚቀርበው መሰዊያ ላይ ያቃጥለዋል፡፡ ካህኑ መስዋእት አቅራቢው የሰራውን ኃጢአት ያስተሰርይለታል፣ እናም ሰውየው ይቅር ይባላል፡፡



Chapter 5

1 ማንም ሰው ያየውንም ሆነ የሰማውን አንዳች ነገር መምስከር ሲገባው ባለመመስከር ኃጢአት ቢሰራ፣ ይጠየቅበታል፡፡ 2 ወይም ማንም ሰው እግዚአብሔር ንጹህ አይደለም ያለውን ማናቸውንም ነገር ቢነካ፣ ይህ ንጹህ ያልሆነ ነገር የዱር እንስሳ ስጋ ወይም የሞተ የቤት እንስሳ ቢሆን፣ ወይም ማናቸውንም ያልነጻ ሰው ቢነካ፣ ደግሞም ይህን ማድረጉን ባያውቅ፣ ስለ ነገሩ ባወቀ ጊዜ ኃጢአጠኛ ይሆናል፡፡ 3 ቁጥር 3 (?) 4 ወይም ማንም ሰው በችኮላ ክፉ ወይም በጎ ለማድረግ በከንፈሮቹ ቢምል፣በችኮላ የማለው መሀላ ምንም አይነት ይሁን፣ ስለ ነገሩ ባያውቅ እንኳን፣ ነገሩን ባወቀ ጊዜ ከእነዚህ በማናቸውም ነገር ኃጢአተኛ ይሆናል፡፡ 5 አንድ ሰው ከእነዚህ ነገሮች በማንኛውም በደለኛ ሆኖ ሲገኝ፣የሰራውን ማንኛውንም ኃጢአት መናዘዝ አለበት፡፡ 6 ከዚያም ለሰራው ኃጢአት የበደል መስዋዕቱን ወደ ያህዌ ማምጣት አለበት፣ ለኃጢአት መስዋዕት ሴት ጠቦት በግ ወይም ሴት ፍየል ያቀርባል፤ ካህኑም ስለ ሰራው ኃጢአት ያስተሰርይለታል፡፡ 7 ጠቦት መግዛት ካልቻለ፣ ለኃጢአቱ የበደል መስዋዕት ለያህዌ ሁለት ዋኖሶች ወይም ሁለት እርግቦች ማምጣት ይችላል፤ አንዱ ለኃጢአት መስዋዕት እና ሌላኛው ለሚቃጠል መስዋዕት ያመጣል፡፡ 8 እነዚህን ወደ ካህኑ ያመጣል፣ እርሱም በመጀመሪያ አንዱን ለኃጢአት መስዋዕት ያቀርባል - እርሱም የመስዋዕቱን ራስ ከአንገቱ ይቆለምማል ነገር ግን ሙሉ ለሙሉ አይለያየውም፡፡ 9 ከዚያ ከኃጢአት መስዋዕቱ ጥቂት ደም ወስዶ በመሰዊያው ጎን ይረጫል፣ ከዚያ የቀረውን ደም በመሰዊያው ስር ደሙን ያንጠፈጥፈዋል፡፡ ይህ የኃጢአት መስዋዕት ነው፡፡ 10 ከዚያ ሁለተኛውን ወፍ በህጉ መሰረት የሚቃጠል መስዋዕት አድርጎ ያቀርበዋል፣ እናም ካህኑ ሰውየው ለሰራው ኃጢአት ማስተስረያ ያደርገዋል፤ ይቅር ይባላል፡፡ 11 “ነገር ግን ሁለት ዋኖሶች ወይም ሁለት እርግቦች መግዛት ሳይችል ቢቀር፣ ለሰራው ኃጢአት የኢፍ መስፈሪያ አንድ አስረኛ መልካም ዱቄት መስዋዕት ያቅርብ፡፡ ያኃጢአት መስዋዕት ስለሆነ ዘይት ወይም ዕጣን አይጨምርበት፡፡ 12 መስዋዕቱን ወደ ካህኑ ያቅርበው፣ካህኑም ለያህዌ በጎነት ምስጋና ለማቅረብ ከዱቄቱ እፍኝ ይወስዳል፣ ከዚያም በመሰዊያው ላይ ለያህዌ በመስዋዕቱ ላይ በእሳት ያቃጥለዋል፡፡ ይህ የኃጢአት መስዋዕት ነው፡፡ 13 ካህኑ ሰውየው የሰራውን ማንኛውንም ኃጢአት ያስተሰርይለታል፤ይቅር ይባላል፡፡ ከመስዋዕት የተረፈው እንደ እህል ቁርባኑ ሁሉ የካህኑ ይሆናል፡፡’” 14 ከዚያም ያህዌ እንዲህ ሲል ሙሴን ተናገረው፣ 15 “ማንም ሰው የያህዌን ትዕዛዝ በመጣስ እርሱ ካለው ውጭ ሆኖ ኃጢአት ቢሰራ፣ ነገር ግን ይህንን ሁን ብሎ ባያደርግ ለያህዌ የበደል መስዋዕት ያቅርብ፡፡ ይህ መስዋዕት ከመንጋው ውስጥ ነውር የሌለበት ዋጋውም ለኃጢአት መስዋዕት በቤተ መቅድስ ገንዘብ በጥሬ ብር መገመት አለበት፡፡ 16 ቅዱስ ከሆነው በማጉደል ለሰራው በደል ዕዳውን በመክፈል ያህዌን ደስ ማሰኘት አለበት፣ እናም አንድ አምስተኛውን በዚህ ላይ ጨምሮ ለካህኑ ይስጥ፡፡ ከዚያ ካህኑ ከበደል መስዋዕቱ ጠቦት ጋር ያስተሰርይለታል፤ እናም ይቅር ይባላል፡፡ 17 ማንም ሰው ኃጢአት ቢሰራና ያህዌ እንዳይደረግ ያዘዘውን ማናቸውንም ነገር ቢያደርግ፣ ምንም እንኳን ነገሩን ሳያውቅ ቢያደርገውም በደለኛ ነው፤ ስለዚህም በበደሉ ጥፋተኛ ነው፡፡ 18 ከመንጋው ውስጥ ነውር የሌለበት ጠቦት ያቅርብ ለካህኑ ለበደል መስዋዕት ተመጣጣኝ ዋጋ ያምጣ፡፡ ከዚያም ካህኑ ሳያውቅ ከሰራው ኃጢአት ያስተሰርይለታል፤ ይቅር ይባላል፡፡ 19 ይህ የበደል መስዋዕት ነው፣ በያህዌ ፊት በእርግጥ ኃጢአተኛ ነው፡፡”



Chapter 6

1 ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 2 “ ማንም ሰው ኃጢአት ቢሰራና የያህዌን ትዕዛዝ ቢተላለፍ፣ ታማኝነቱን አፍርሶ ሃሰተኛ ቢሆን፣ ወይም ጎረቤቱ በአደራ የሰጠውን ቢክድ፣ ወይም ቢያታልል ወይም ቢሰርቀው፣ወይም ጎረቤቱን ቢበድል 3 ወይም ከጎረቤቱ የጠፋ ነገር አግኝቶ ቢዋሽ፣ እናም በሃሰት ቢምል፣ ወይም እነዚህን በመሰሉ ሰዎች በሚበድሉባቸው ጉዳዮች ኃጢአት ቢሰራና፣ 4 በደለኛ ሆኖ ቢገኝ፣ በስርቆት የወሰደውን ይመልስ ወይም የበደለውን ይካስ፣ ወይም ታማኝነቱን አጉድሎ የወሰደውን ጠፍቶ ያገኘውን ነገር ይመልስ፡፡ 5 ወይም በማንኛውም ጉዳይ ላይ ቢዋሽ፣ ሙሉ ለሙሉ ይመልስ፤ እንዲሁም ጥፋተኛ ሆኖ በተገኘ ጊዜ ለባለንብረቱ አንድ አምስተኛውን ጨምሮ ይክፈል፡፡ 6 ከዚያም የበደል መስዋዕቱን ዋጋው ተመጣጣኝ የሆነ ነውር የሌለበት ጠቦት ከመንጋው የኃጢአት መስዋእት ለያህዌ ወደ ካህኑ ያምጣ፡፡ 7 ካህኑ የኃጢአት ማስተስረያ በያህዌ ፊት ያቀርባል፣ እናም በዳዩ ለሰራው በደል ሁሉ ይቅር ይባላል፡፡” 8 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 9 “አሮንን እና ልጆቹን እንዲህ ብለህ እዘዛቸው፣ ‘የሚቃጠል መስዋዕት ህግ ይህ ነው፡ የሚቃጠለው መስዋዕት በመሰዊያው ምድጃ ላይ ሌሊቱን ሁሉ እስከ ማለዳ ይገኝ፣ ደግሞም የመሰዊያው እሳት ሳያቋርጥ ይንደድ፡፡ 10 ካህኑ የበፍታ ልብሱን ይልበስ፣ እንዲሁም የበፍታ ቀሚን ይልበስ፡፡ እሳቱ በመሰዊያው ላይ ያለውን የሚቃጠለውን መስዋዕት ከበላ በኋላ አመዱን ይፈስ፣ ከዚያም አመዱን ከመሰዊያው ጎን ይድፋው፡፡ 11 አመዱን ከሰፈር ውጭ ንጹህ ወደ ሆነ ስፍራ ለመውሰድ የለበሰውን አውልቆ ሌላ ልብስ ይልበስ፡፡ 12 በመሰዊው ላይ ያለው እሳት ሳያቋርጥ ይንደድ፡፡ መጥፋት የለበትም፣ እናም ካህኑ በየማለዳው እንጨት ይጨምርበት፡፡ እንደ አስፈላጊነቱ በላዩ የሚቃጠል መስዋዕት ያድርግበታል፣ ደግሞም የሰላም መስዋዕት ስብ በላዩ ያቃጥልበታል፡፡ 13 እሳቱ ሳያቋርጥ በመሰዊያው ላይ ይንደድ፤መጥፋት የለበትም፡፡ 14 የእህል ቁርባን ህግ ይህ ነው፡፡ የአሮን ልጆች ከያህዌ ፊት በመሰዊያው ላይ ያቀርቡታል፡፡ 15 ካህኑ የእህል ቁርባን አድርጎ እፍኝ መልካም የእህል ዱቄትና ዘይት እንዲሁም ዕጣን ለመስዋዕት ይውሰድና የያህዌን በጎነት ምስጋና ለማቅረብ በመሰዊያው ላይ ያቃጥለው፡፡ 16 አሮንና ልጆቹ ከመስዋዕቱ የቀረውን ይመገቡት፡፡ ይህም እርሾ ሳይገባበት በተቀደሰው ስፍራ ይብላ፡፡ በመገናኛው ድንኳን ቅጽረ ግቢ ይመገቡት፡፡ 17 በእርሾ መጋገር የለበትም፡፡ እኔ በእሳት የተዘጋጀ ድርሻ አድርጌ ሰጥቻቸዋለሁ፡፡ የኃጢአት መስዋዕትና የበደል መስዋዕት እጅግ የተቀደሰ ነው፡፡ 18 ለሚመጣው ተውልድ ሁሉ ለዘመናት ሁሉ ወንድ የሆነ የአሮን ትውልድ ድርሻው አድርጎ ከያህዌ ከሚቀርበው የእሳት ቁርባን ሊበላው ይችላል፡፡ ማናቸውም እርሱን የሚነካ ቅዱስ ይሆናል፡፡” 19 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 20 “ይህ አሮንና ልጆቹ የሚያቀርቡት መስዋዕት ነው፣ እያንዳንዳቸው የአሮን ልጆች በሚቀቡበት ቀን ለያህዌ የሚያቀርቡት መስዋዕት ነው፡፡ እንደ ተለመደው የእህል ቁርባን የኢፍ አንድ አስረኛ ክፍል መልካም ዱቄት፤ በጠዋት ግማሹን የተቀረውን ግማሽ ደግሞ ምሽት ያቀርቡታል፡፡ 21 በመጥበሻ ላይ በዘይት ይጋገራል፡፡ በእርጥቡ ሳለ፣ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ እንዲሆን ታቀርበዋለህ፡፡ የእህል ቁርባኑን ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ እንዲሆን ቆራርሰህ ታቀርበዋለህ፡፡ 22 ከሊቀ ካህኑ ልጆች መሃል ተተኪ ካህን የሚሆነው ወንድ ልጅ መስዋዕቱን ያቀርባል፡፡ ለዘለዓለም እንደታዘዘው፣ መስዋዕቱ በሙሉ ለያህዌ ይቃጠላል፡፡ 23 ካህኑ የሚያቀርበው እያንዳንዱ የእህል ቁርባን ሙሉ ለሙሉ ይቃጠላል፤አይበላም፡፡” 24 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 25 “አሮንና ወንዶች ልጆቹን እንዲህ በላቸው፣ ‘የኃጢአት መስዋዕት ህግ ይህ ነው፡ የኃጢአት መስዋዕት የሚታረደው የሚቃጠል መስዋዕት በሚታረድበት ስፍራ ያህዌ ፊት ነው፡፡ እጅግ ቅዱስ ነው፡፡ 26 የኃጢአት መስዋዕት የሚያቀርበው ካህን ይመገበዋል፡፡ በመገናኛው ድንኳን ቅጽረግቢ በተቀደሰው ስፍራ ይበላ፡፡ 27 የመስዋዕቱን ስጋ የሚነካ ሁሉ ይቀደሳል፣ደሙ በየትኛውም ልብስ ላይ ቢረጭ ደሙ የነካውን የጨርቁን ስፍራ በተቀደሰ ቦታ እጠበው፡፡ 28 የተቀቀለበት የሸክላ ማሰሮ ግን ይሰበር፡፡ 29 ከካህናቱ መሀል ማናቸውም ወንድ ከዚህ መብላት ይችላል ምክንያቱም እጅግ ቅዱስ ነው፡፡ 30 በተቀደሰው ስፍራ ወደ መገናኛው ድንኳን ለማስተስረይ ደሙ ከቀረበው የኃጢአት መስዋዕት ምንም አይበላ፡፡



Chapter 7

1 የበደል መስዋዕት ህግ ይህ ነው፡፡ እጅግ ቅዱስ ነው፡፡ 2 የበደል መስዋዕቱን በሚታረድበት ስፍራ የበደሉንም መስዋዕ ይረዱት፣ ደሙን በመሰዊያው እያንዳንዱ ጎን ይርጩት፡፡ 3 በመስዋዕቱ ከብት ውስጥ ያለው ስብ ሁሉ ይቃጠል፤ ላቱ፣የሆድ ዕቃውን ክፍሎች የሸፈነው ስብ በመሁሉ፣ 4 በጎድኑ አጠገብ ያለው ስብ፣ ሁለቱ ኩላሊቶችና በላያቸው ያለው ስብ፣ ጉበቱን የሸፈነው ስብ፣ ከኩላሊቶቹ ጋር - እነዚህ ሁሉ ይቅረቡ፡፡ 5 ካህኑ እነዚህን ክፍሎች በእሳት የተዘጋጀ መስዋዕት አድርጎ በመሰዊያው ላይ ለያህዌ ያቃጥል፡፡ ይህ የበደል መስዋዕት ነው፡፡ 6 እያንዳንዱ ካህን ከዚህ መስዋዕት መብላት ይችላል፡፡ በተቀደሰ ስፍራ ይበላ ምክንያቱም እጅግ ቅዱስ ነው፡፡ 7 የኃጢአት መስዋዕት ልክ እንደ በደል መስዋዕት ነው፡፡ የሁለቱም ህግ ተመሳሳይ ነው፡፡ እነዚህ ህጎች የማስተስረይ አገልግሎት ለሚሰጡ ካህናት ያገለግላሉ፡፡ 8 የየትኛውንም ሰው የሚቃጠል መስዋዕት የሚያቀርብ ካህን የመስዋዕቱን ቆዳ መውሰድ ይችላል፡፡ 9 በምድጃ የሚዘጋጅ እያንዳንዱ የእህል ቁርባን፣ እና በመጥበሻ የሚዘጋጅ እንዲህ ያለው እያንዳንዱ መስዋዕት ወይም በመጋገሪያ መጥበሻ ላይ የሚዘጋጅን መስዋዕት፣ መስዋዕቱን የሚያሳርገው ካህን ይወስደዋል፡፡ 10 ደረቅም ሆነ በዘይት የተለወሰ እያንዳንዱ የእህል ቁርባን ለአሮን ትውልዶች እኩል የእነርሱ ነው፡፡ 11 ይህ ሰዎች ለያህዌ የሚያቀርቡት የሰላም መስዋዕት ህግ ነው፡፡ 12 ማንም ሰው ምስጋና ለማቅረብ ይህን ቢያደርግ፣ እርሾ የሌለበት መስዋዕት አድርጎ ያቅርበው፣ ነገር ግን ቂጣውን በዘይት ይለውሰው፣ ቂጣው በመልካም ዱቄት የተዘጋጀ በዘይት የተለወሰ ይሁን፡፡ 13 ደግሞም ምስጋና ለማቅረብ፣ ከሰላም መስዋዕቱ ጋር በእርሾ የተዘጋጀ ህብስት ያቅርብ፡፡ 14 ከእነዚህ መስዋዕቶች ከእያንዳንዳቸው አንድ አይነት መስዋዕት ለያህዌ ያቅርብ፡፡ ይህ የሰላም መስዋዕቱን ደም በመሰዊያው ላይ ለሚረጩት ካህናት ይሰጥ፡፤ 15 ምስጋና ለማቅረብ የሰላም መስዋዕት የሚያቀርበው ሰው መስዋዕቱ በሚቀርብበት ዕለት የመስዋዕቱን ስጋ ይብላ፡፡ ከስጋው እስከ ማግስቱ አይደር፡፡ 16 ነገር ግን መስዋዕቱ የሚያቀርበው ለስዕለት ከሆነ፣ ወይም በበጎ ፈቃድ የሚቀርብ መስዋዕት ከሆነ ስጋው መስዋዕቱን ባቀረበበት ዕለት ባያልቅ በማግስቱ ሊበላ ይችላል፡፡ 17 ሆኖም፣ ከመስዋዕቱ የተረው ስጋ በሶስተኛው ቀን ይቃጠል፡፡ 18 አንድ ሰው ካቀረበው የበጎ ፈቃድ መስዋዕት አንዳች ስጋ በሶስተኛው ቀን ቢበላ ይህ ተቀባይነት የለውም፤ መስዋዕቱን ላቀረበውም ዋጋ የለውም፡፡ ደስ የማያሰኝ ነገር ይሆናል፣ ስጋውን ለሚበላውም ሰው የበደል ዕዳ ይሆንበታል፡፡ 19 ንጹህ ያልሆነ ነገር የነካ ከዚህ ስጋ አይበላም፡፡ ስጋው መቃጠል ይኖርበታል፡፡ የተረውን ስጋ፣ ማንኛውም ንጹህ የሆነ ሰው ሊበላው ይችላል፡፡ 20 ሆኖም፣ ለያህዌ የሚቀርበውን የሰላም መስዋዕት ስጋ የበላ ንጹህ ያልሆነ ሰው ከህዝቡ ተለይቶ ይወገድ፡፡ 21 ማንኛውም ሰው ንጹህ ያልሆነ ነገር ቢነካ - ንጹህ ያልሆነን ሰው፣ ወይም ንጹህ ያልሆነን አውሬ፣ ወይም ንጹህ ያልሆነ እና ደስ የማያሰኝ ነገር ቢነካ፣ እና ከዚያም ለያህዌ ከቀረበው የሰላም መስዋዕት ስጋ ቢበላ ያሰው ከህዝቡ ተለይቶ ይወገድ፡፡ 22 ቀጥሎም ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 23 “የእስራኤልን ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‘የበሬ ወይም የበግ ወይም የፍየል ስብ አትብሉ፡፡ 24 ሳይታረድ ሞቶ የተገኘ እንስሳ ስብ፣ ወይም በዱር አውሬ የተገደለ እንስሳ ስብ ለሌላ ተግባር ሊውል ይችላል፣ ነገር ግን የዚያን እንስሳ ስብ በፍጹም አትብሉ፡፡ 25 ሰዎች በእሳት ለያህዌ መስዋዕት አድርገው ሊያቀርቡ የሚችሉትን እንስሳ ስብ የሚላ ማንኛውም ሰው፣ ከህዝቡ ተለይቶ ይወገድ፡፡ 26 በቤቶቻችሁ የወፍም ሆነ የእንስሳ ማናቸውም ዐይነት ደም አትብሉ፡፡ 27 ማናቸውንም ደም የበላ ማንም ሰው፣ ከህዝቡ ተለይቶ ይጥፋ፡፡’” 28 ደግሞም ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 29 “የእስራኤልን ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‘ለያህዌ የሰላም መስዋዕት የሚያቀርብ ከመስዋዕቱ ላይ ወስዶ ለያህዌ ያቅርብ፡፡ 30 ለያህዌ በእሳት የሚዘጋጀውን መስዋዕት፣ በእርሱ በራሱ እጅ ያቅረበው፡፡ ስቡን ከፍርምባው ጋር ያቅርበው፣ ስለዚህ ፍርምባውን በያህዌ ፊት ለመስዋዕት ያቅርበው፡፡ 31 ካህኑ ስቡን በመሰዊያ ላይ ያቃጥለው፣ ነገር ግን ፍርምባው የአሮንና የትውልዱ ነው፡፡ 32 የቀኙን ወርች ከሳለም መስዋዕታችሁ የቀረበ ስጦታ አድርጋችሁ ለካህኑ ስጡት፡፡ 33 የሰላም መስዋዕቱንና ስቡን ደም የሚያቀርበው ከአሮን ትውልድ ውስጥ የሆነው ካህን ከመስዋዕቱ ውስጥ የቀኝ ወርቹ የእርሱ ድርሻ ነው፡፡ 34 ለእኔ የተወዘወዘውንና የቀረበውን የፍርምባውንና የወርቹን መስዋዕት እኔ ስለ ወሰድኩ፣ እነዚህን ሊቀካህን ለሆነው ለአሮንና ለዘሩ ሰጥቻለሁ፣ ይህ ሁልጊዜም በእስራኤል ህዝብ ከሚዘጋጀው የሰላም መስዋዕት ድርሻቸው ይሆናል፡፡ 35 ሙሴ በካህናት አገልግሎት ያህዌን እንዲያገለግሉ እነርሱን ባቀረበ ቀን ይህ ለአሮንና ለዘሮቹ በእሳት ለያህዌ ከሚቀርበው መስዋዕት ድርሻቸው ነው፡፡ 36 እርሱ ካህናትን በቀባ ቀን ያህዌ ከእስራኤል ህዝብ ድርሻቸው ሆኖ ለእነርሱ እንዲሰጥ ያዘዘው ይህ ነው፡፡ ይህ ሁልጊዜም በትውልዶች ሁሉ ድርሻቸው ይሆናል፡፡ 37 ይህ የሚቃጠል መስዋዕት፣ የእህል ቁርባን፣ የኃጢአት መስዋዕት፣ በደል መስዋዕት፣ የክህነት ሹመት መስዋዕት እና የሰላም መስዋዕት ስርዓት ነው፤ 38 ይህ ያህዌ ለሙሴ በሲና ተራራ ላይ የእስራኤል ህዝብ መስዋዕታቸውን በሲና ምድረበዳ የሚያቀርቡበትን ህግጋት ለሙሴ በሰጠበት ቀን የተሰጠ ስርዓት ነው፡፡



Leviticus 7:22

እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤ ለእስራኤላዊያን እንዲህ በላቸው፤ “…ሥብ አትብሉ”::

ይህ በጥቅስ ውስጥ የተጠቀሰ ጥቅስ ነው፡፡ ቀጥተኛው ጥቅስ እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊወሰድ ይችላል፡፡ አት፤ ከዚያም እግዚአብሔር ለሙሴ ተናገረ እናም ለእግዚአብሔር ሕዝብ እንዲናገር እንዲህ አለው፤ “…ሥብ አትብሉ”:: (ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶች ይመልከቱ)

ሳይሠዋ ሞቶ የተገኘውን

“የሞተ ነገር ግን መሥዋዕት ያልሆነውን”

በአውሬዎች የተገደለ ከብት ሥብ

ይህ በተሻጋሪ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “አውሬዎች የገደሉት ከብት ሥብ”:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ለሌላ ተግባር ይዋል

ይህ በተሻጋሪ ግሥ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት “ለሌላ ተግባር ያውሉት”:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ::)

Leviticus 7:25

በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል አት “የሚቃጠል መሥዋዕት”

ያ ሰው ከሕዝቡ ይወገድ

ያ ሰው ከሕዝቡ ዘንድ መወገድ ብጣሽ ጨርቅ ወይም የዛፍ ቅርንጫፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ ዘንድ እንደተቆረጠ ተደርጐ ተገልጾአል:: ይህ በተሻጋሪ ግሥ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: በዘሌዋዊያን 7:2ዐ ይህን እንዴት እንደተረጐመ ይመልከቱ:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ደም አትብሉ “ደምን አትመገቡ”

በማንኛውም ቤቶቻችሁ “በየትኛውም ቤቶቻችሁ” ወይም “በማንኛውም በሚትኖሩበት ቦታ”

Leviticus 7:28

ስለዚህ እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው ለእስራኤላዊያን እንዲህ በላቸው መሥዋዕት የሚያቀርብ ማንኛውም ሰው

ይህ በጥቅስ ውስጥ የተጠቀሰ ጥቅስ ነው፡፡ ቀጥተኛው ጥቅስ እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊወሰድ ይችላል፡፡ አት “ከዚያም እግዚአብሔር ሙሴን ተናገረ፤ እናም ለእስራኤል ሕዝብ እንዲናገር እንዲህ አለው፤ መሥዋዕት የሚያቀርብ ማንኛውም ሰው፤”(ጥቅሶችን በጥቅስ ውስጥና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶች ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር የሚያቀርበውን መሥዋዕት በራሱ እጅ ያቅርበው

በራሱ እጅ ያቅርበው የሚለው አባባል በዐረፍተ ነገሩ መጀመሪያ ሊቀመጥ ይችላል በእሳት ያቅርበው የሚለው ሀረግ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል አት ፤ እርሱ ራሱ መሥዋዕት አድርጐ ለማቃጠል ያቀደውን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር ያቅርበው፤ (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ::)

በራሱ እጅ ያቅርበው

እዚህ “እጅ” መላውን ሰው ያመለክታል:: አት “እርሱ ራሱ ያቅርበው” (see synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ እናም ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዜይቤያዊ አነጋገር ወይም ሥዕላዊ መግለጫ ይመልከቱ)::

ፍርምባ

የአንድ እንስሳ ከአንገት በታች ፊተኛ የአካል ክፍል ነው

ፍርምባውን መሥዋዕት አድርጐ በእግዚአብሔር ፊት ይወዘውዘው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ ካህኑ ይህን ለእግዚአብሔር የሚወዘወዝ መሥዋዕት አድርጐ ሊያቀርብ ይችላል:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)፡፡

በእግዚአብሔር ፊት የሚወዘወዝ መሥዋዕት ተደርጐ ሊወዘወዝ ይችላል፤

መሥዋዕቱን ከፍ አድርጐ መያዝ ሰውየው መሥዋዕቱን ለእግዚአብሔር ማቅረቡ የሚያመለክት ምልክት ነው፡፡ (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)::

Leviticus 7:31

ወርች

ከጉልበት በላይ ያለው የእንስሳ አካል ክፍል ነው

እንደ መሥዋዕት ይቀርባል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እና ይህ መሣዋዕት ተደርጐ ይቅረብ”፤ (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)፡፡

Leviticus 7:33

እኔ ወስጃለሁ

እዚህ “እኔ” እግዚአብሔርን ያመለክታል::

ይህ የሚሰጥ ድርሻ

“ያም እንደመሥዋዕት የሚሰጥ”

Leviticus 7:35

በእሳት ለእግዚአብሔር ከቀረበው መሥዋዕት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት ነው:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)፡፡

እስራኤላዊያን እንዲሰጧቸው እግዚአብሔር አዘዘ፡፡

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ ያም ለእነርሱ እንዲሰጡ እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ አዘዘ:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)፡፡

ካህናቱን በቀባበት

“ሙሴ ካህናቱን በቀባበት”

ከትውልድ እስከ ትውልድ

በዘሌዋዊያን 3:17 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

Leviticus 7:37

አገናኝ ዐረፍተነገር

ይህ በዘሌዋዊያን 7:29 የተጀመረው ንግግር ማብቂያ ነው::


Chapter 8

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “አሮንንና ልጆቹን፣ የክህነት ልብሶቹን፣ የቅባት ዘይቱን፣የኃጢአት መስዋዕቱን ወይፈኖች፣ ሁለቱን ጠቦቶች፣ እርሾ የሌለበትን ህብስት መሶብ ከእርሱ ጋር ውሰድ፡፡ 3 በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ ሁሉንም ጉባኤ ሰብስብ፡፡” 4 ስለዚህም ሙሴ ያህዌ እንዳዘዘው አደረገ፣ ጉባኤውም በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ ተሰበሰበ፡፡ 5 ከዚያም ሙሴ ለጉባኤው እንዲህ አለ፣ “ያህዌ እንዲደረግ ያዘዘው ይህ ነው፡፡” 6 ሙሴ አሮንንና ልጆቹን አቀረበና በውሃ አጠባቸው፡፡ 7 አሮንን እጀ ጠባብ አለበሰውና በወገቡ ዙሪያ መቀነት አስታጠቀው፣ ቀሚ አጠለቀለትና ኤፉድ ደረበለት፣ ከዚያም ኤፉዱን በጥበብ በተጠለፈ መቀነት አስታጠቀው፡፡ 8 በቀሚሱ ላይ ደረት ኪስ አደረገለት፣ በደረት ኪሱ ውስጥ ኡሪምና ቱሚም አደረገበት፡፡ 9 ሙሴ ያህዌ እንዳዘዘው በራሱ ላይ ጥምጥሙን ጠመጠመለት፣ በጥምጥሙ ላይ ከፊት በኩል ወርቃማ ቅብና ቅዱስ አክሊል አደረገለት፡፡ 10 ሙሴ የቅባቱን ዘይት ወሰደ፣ ማደሪያ ድንኳኑንና በውስጡ ያለውን ሁሉ ቀባው፤ እናም ለያህዌ ቀደሳቸው፡፡ 11 በመሰዊያው ላይ ዘይቱን ሰባት ጊዜ ረጨው፣ እናም መሰዊያውንና መገልገያዎቹን ሁሉ ቀባቸው፣ እንዲሁም የመታጠቢያ ሳህኑንና ማስቀመጫውን፣ ለያህዌ ቀደሳቸው፡፡ 12 አሮንን ያህዌ ለመለየት ከቅባቱ ዘይት ጥቂቱን በአሮን ራስ ላይ አፈሰሰው፡፡ 13 ሙሴ ያህዌ እንዳዘዘው የአሮንን ወንድ ልጆች አቅርቦ እጀጠባብ አለበሳቸው፣ በወገባቸው ዙሪያ መታጠቂያ አሰረላቸው፣ በራሳቸው ላይ በፍታ ጨርቅ ጠቀለለላቸው፡፡ 14 ሙሴ ለኃጢአት መስዋዕት በሬ አመጣ፣ አሮንና ልጆቹ ለኃጢአት መስዋዕት ባመጡት በሬ ላይ እጆቻቸውን ጫኑ፡፡ 15 በሬውን አርዶ ደሙን በመሰዊያው ቀንዶች ውስጥ በጣቱ ጨመረ፣ በመሰዊያው ስር ደሙን አፈሰሰ፣ ለማስተስረይ ለእግዚአብሔር ለየው፡፡ 16 በመስዋዕቱ ሆድ ዕቃ ውስጥ ያለውን ስብ ሁሉ አወጣ፣ በጉበቱ መሸፈኛና በሁለቱ ኩላሊቶች ላይ ያለውን ስብ ወስዶ በመሰዊያው ላይ ሁሉንም አቃጠለው፤ 17 ነገር ግን በሬውን፣ ቆዳውን፣ ስጋውን እና ፈርሱን ያህዌ እንዳዘዘው ከሰፈር አውጥቶ አቃጠለው፡፡ 18 ሙሴ ለሚቃጠል መስዋዕት ጠቦቱን አቀረበ፣ አሮንና ልጆቹ በጠቦቱ ራስ ላይ እጃቸውን ጫኑ፡፡ 19 ሙሴም ጠቦቱን አርዶ በመሰዊያው ዙሪያ ደሙን ረጨ፡፡ 20 ጠቦቱን ቆራርጦ ራሱንና ቁርጥራጩን እንዲሁም ስቡን አቃጠለ፡፡ 21 የሆድ ዕቃውን ክፍሎችና እግሮቹን በውሃ አጠበ፣ ከዚያም ጠቦቱን በሙሉ በመሰዊያው ላይ አቃጠለ፡፡ ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው ይህ የሚቃጠል መስዋዕት ነው፤ ደግሞም ለያህዌ በእሳት የተዘጋጀ ጣፋጭ መዓዛ ነው፡፡ 22 ከዚያም ሙሴ ሌላውን ጠቦት ያቀርባል፣ ይህም የክህነት ሹመት መስዋዕት ነው፣ እናም አሮንና ልጆቹ በጠቦቱ ራስ ላይ እጃቸውን ይጭናሉ፡፡ 23 አሮን ጠቦቱን ያርዳል፣ ሙሴም ከደሙ ጥቂት ወስዶ በአሮን ቀኝ ጆሮ ጫፍ ላይ፣ በቀኝ እጁ አውራ ጣት እና በቀኝ እግሩ አውራ ጣት ላይ ያደርጋል፡፡ 24 የአሮንን ልጆች አቅርቦ፣ በቀኝ ጆሯቸው ጫፍ ላይ፣ በቀኝ እጃቸው አውራ ጣት ላይ እና በቀኛ እግራቸው አውራ ጣት ላይ ከደሙ ጥቂት ወስዶ ያደርጋል፡፡ ከዚያ ሙሴ የበጉን ደም በመሰዊያው ጎኖች ሁሉ ይረጫል፡፡ 25 ስቡን፣ ላቱን፣ በሆድ ዕቃ ክፍሎች ውስጥ ሁሉ የሚገኘውን ስብ፣ የጉበቱን መሸፈኛ፣ ሁለቱን ኩላሊቶች እና በላያቸው የሚገነውን ስብ እንዲሁም ቀኝ ወርቹን ወሰደ፡፡ 26 በያህዌ ፊት ከነበረው መሶብ እርሾ የሌለበት አንድ ህብስት ይወስዳል፣ደግሞም በዘይት ተለውሶ ከተሰራው ዳቦ አንዱን እና አንድ ስስ ቂጣ ይውሰድና በስቡና በቀኝ ወርች ላይ ያኖረዋል፡፡ 27 ሁሉንም በአሮን እጆችና በአሮን ወንድ ልጆች እጆች ላይ ያስቀምጠዋል፣ ይህንንም ለሚወዘወዝ መስዋዕት በያህዌ ት ያቀርባሉ፡፡ 28 ከዚያም ሙሴ ከእጃቸው ይወስድና የሚቃጠል መስዋዕት አድርጎ ያቀርበው፡፡ እነዚህ የክህነት ሹመት መስዋዕት ናቸው፤ ጣፋጭ መዓዛ ሆነው ይቀርባሉ፡፡ ይህ በእሳት ለያህዌ የሚቀርብ መስዋዕት ነው፡፡ 29 ሙሴ ፍርምባውን ወስዶ ለያህዌ መስዋዕት አድርጎ ይወዝውዘው፡፡ ያህዌ እንዳዘዘው ይህ ከጠቦቱ የክህነት ሹመት የሙሴ ድርሻ ነው፡፡ 30 ሙሴ በመሰዊያው ላይ ካለው ከቅባት ዘይቱና ከደሙ ጥቂት ወስዶ እነዚህን በአሮን ላይ፣ በልብሶ ላይ፣ በወንድ ልጆቹ ላይ እና ከእርሱ ጋር በልጆቹ ልብሶች ላይ ይረጫል፡፡ በዚህ መንገድ አሮንና የክህነት ልብሱን እንዲሁም ልጆቹንና ልብሳቸውን ለያህዌ ይቀድሳል፡፡ 31 ደግሞም ሙሴ ለአሮንና ለልጆቹ እንዲህ አለ፣ “በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ ስጋውን ቀቅሉት፣ በዚያም ስፍራ በሹመት መስጫው መሶብ ውስጥ ያለውን ህብስትም ‘አሮንና ልጆቹ ይብሉት’ ብዬ እንዳዘዝኩት ብሉት፡፡ 32 ከስጋውና ከህብስቱ የተረፈውን በሙሉ አቃጥሉት፡፡ 33 የሹመት ስርዓቱ እስኪጠናቀቅ ድረስ ለሰባት ቀናት ከመገናኛው ከመገናኛው ድንኳን መግቢያ አትለፉ፡፡ ያህዌ በሰባት ቀናት ውስጥ ይሾማችኋል፡፡ 34 በዚህ ቀን የሚሆነው እናንተን ለማስተረይ ያህዌ እንዲደረግ ያዘዘው ነው፡፡ 35 ለሰባት ቀናት ቀንም ሆነ ሌሊት በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ ትቆያላችሁ፣ ደግሞም የያህዌን ትዕዛዝ ትጠብቃላችሁ፣ ይህን ካደረጋችሁ አትሞቱም፣ ምክንያቱም የታዘዝኩት ይህንን ነው፡፡” 36 ስለዚህም አሮንና ልጆቹ ያህዌ በሙሴ በኩል እንዲያደርጉት ያዘዛቸውን ሁሉንም ነገር አደረጉ፡፡



Leviticus 8:1

አጠቃላይ መረጃ

በዘጸአት መጽሐፍ በሙሴ በዘገበው የእግዚአብሔር ትዕዛዝ መሠረት በምዕራፍ 8 ሙሴ አሮንና ልጆቹን ካህናት አድርጐ ይሾማቸዋል፡፡

ልብሰ ትክህኖ

“የካህናት ልብሶች” ወይም “ካህናት የሚለብሱት ልብሶች”

Leviticus 8:4

እግዚአብሔር እንዲደረግ ያዘዘው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፤ አት፤ እግዚአብሔር እንድናደርገው ያዘዘን (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)፡፡

Leviticus 8:6

በውሃም አጠባቸው

ይህ ምልክታዊ ድርጊት ነው:: ይህም ካህናት እንዲሆኑ የሚያዘጋጃቸው የመንጻት ሥርዓት ነው፤ (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)::

ቀሚስ ፤እጀ ጠባብ፤ መቀነት፤ ኤፋድ፤ በልዩ ጥበብ የተጠለፈ መታጠቂያ‹፤

እነዚህ ልዩ አልባሳት ሕዝቡ ለካህናት እንዲያዘጋጁ እግዚአብሔር ያዘዛቸው ናቸው:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃዎች ይመልከቱ)::

መቀነት

በወገብ ወይም በደረት የሚታሠር ቀጭን ረጅም ልብስ ነው፡፡

አስታጠቀው

“በላዩም አሰረው”

Leviticus 8:8

የደረት ኪሱን በላዩ አደረገለት

“ሙሴ ለአሮን የደረት ኪስ በላዩ አደረገለት”

የደረት ኪስ፤ ጥምጥም፤ ወርቃማ ቆብ፤ ቅዱስ አክሊል

እነዚህ ልዩ አልባሳት ሕዝቡ ለካህናት እንዲያዘጋጁ እግኢብሔር ያዘዛቸው ናቸው:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃዎች ይመልከቱ)::

ኡሪም እና ቱሚም

እነዚህ ነገሮች ምን እንደሆኑ ግልጽ አይደሉምና መገለጽ አለባቸው ካህኑ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ የሚጠቀማቸው ዕቃዎች ናቸው፡፡ (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ጥምጥም

የሰው ራስ የሚሸፍንና በዙሪያውን የሚጠመጠም በረጅም የተቆረጠ ጨርቅ ነው፡፡

ወርቃማ ቆብና ቅዱስ አክልል

ሁለቱ ሀረጐች አንድን ነገር የሚገልጹ ናቸው ንጹህ የወርቅ ቆብ ከጥምጥሙ ጋር ተያይዞ ይገኛል::

Leviticus 8:10

የመሠዊያው መገልገያ ዕቃዎች ሁሉ

እነዚህም ማሠሮዎች ምጣዶች ወይም ሳህኖች መቆስቆሻዎችና ሹካዎች ሁሉ፤

የመታጠቢያ ሳህን

ይህ በመሠዊያውና በታቦቱ መካከል የሚገኝ የመዳብ ሳህን ነው፡፡

ይህ በመሠዊያውና በታቦቱ መካከል የሚገኝ የመዳብ ሳህን ነው፡፡ የሳህኑ መቀመጫ

ይህ የመታጠቢያው ሳህን የሚቀመጥበት የመዳፍ መቆሚያ ነው፡፡

Leviticus 8:12

አፈሰሰው

ሙሴ አፈሰሰው::

መታጠቂያዎች

ይህ መታጠቂያ በብዙነት ሲገለጽ ነው፡፡ በዘሌዋዊያን 8፡7 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

Leviticus 8:14

በወይፈኑ ራስ ላይ እጃቸውን ጫኑ

አሮንና ልጆቹን መሥዋዕት ከሚያቀርቡት እንስሳ ጋር የሚያስመስል ምልክታዊ ድርጊት ነው:: በዚህ መንገድ በእንስሳው በኩል ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ያቀርባሉ:: በዘሌዋዊያን 1:4 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ምልክታዊ ድርጊቶችን ይመልከቱ)

የመሠዊያው ቀንዶች

ይህ የመሠዊያው ማዕዘኖችን ያመለክታል:: በበሬ ቀንድ መልክ የተቀረጹ ናቸው:: በዘሌዋዊያን 4:7 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመለከቱ::

ለእግዚአብሔር ይቀድሰው

“መሠዊያውን ለእግዚአብሔር ይለየው”

እንዲህ አድርጐ ያስተሠርይለት ዘንድ

እዚህ ማስተሠርየት ማለት ወሠዊያውን ለእግዚአብሔር አገልግሎት ጥቅም ብቁ ማድረግ ነው:: አት ለኃጠአት መሥዋዕቶች መቃጠል ቦታውን ምቹ ለማድረግ ነው::

Leviticus 8:16

የውስጥ የሆድ ዕቃዎች

ሆድንና ጨጓራዎችን ነው:: በዘሌዋዊያን 1:9 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ጉበት…. ኩላልቶች

በዘሌዋዊያን 3፡4 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ቆዳ

ቁርበት ወይም የቤት እንስሳት ቆዳ፤

Leviticus 8:18

እጃቸውን በበጉ ላይ ጫኑ

ይህም አሮንና ልጆቹ መስዋዕት የሚያቀርቡት እንስሳ መመሰላቸውን የሚገልጽ ምልክታዊ ድርጊት ነው፡፡ በዚህ መንገድ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርገው ያቀርባሉ:: በዘለዋዊያን 1;4 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Leviticus 8:20

እርሱ በጉን ቆራረጠ

ሙሴ በጉን ቆራረጠ

ሽታውም ደስ ሚያሰኝ

እግዚአብሔር መሥዋዕትን በማቅረብ በቅንነት በሚያመልከው ሰው እንደሚደሰት በሚቃጠል መሥዋዕት ሽታ እንደተደሰተ ተደርጐ ተገልጾአል:: በዘሌዋዊያን 1:9 የዚህ ተመሳሳይ ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ::

ለእግዚአብሔር በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊገለጽ ይችላል:: አት፤ እርሱ ለእግዚአብሔር ያቃጠለው መሥዋዕት: ተሻጋሪ ግሥ የያዘ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ::

Leviticus 8:22

ለቅድስና የሚሆነው አውራ በግ

“ቅድስና” የሚለው ቃል ረቂቅ ስም ነው አት “አሮንና ለጆቹን ለእግዚአብሔር አገልግሎት ለይቶ የሚያቀርብ አውራ በግ” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

እጆቻቸውን በቤጉ ራስ ላይ የጫኑ

ይህም አሮንና ልጆቹ መስዋዕት በሚያቀርቡት እንስሳ መመሰላቸውን የሚገልጽ ምልክታዊ ድርጊት ነው፡፡ በዚህ መንገድ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርገው ያቀርባሉ:: በዘሌዋዊያን 1;4 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

ሙሴ ከደሙም ጥቂት ወስዶ

ደሙ ከእንስሳው እንደወጣ ሙሴ በሳህን እንደያዘው የሚያመለክት ነው የዚህ ዐረፍት ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ

Leviticus 8:25

ውስጠኛ ወይም ሆድ ዕቃዎች

ሆድና ጨጓራዎችን ነው፡፡ ይህን በዘሌዋዊያን 1:9 እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ጉበት…ኩላሊቶች

በዘሌዋዊያን 3:4 እንዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ቀኝ ወርች

ከጉልበት በላይ የሚገኝ የእግር አካል ክፍል፤ በዘሌዋዊያን 7፡32 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

በእግዚአብሔር ፊት ካለው ያለ እርሾ የተጋገረ ዳቦ ካለበት መሶብ

ይህ በመሶብ ያለው ዳቦ ያለበትን ቦታ የሚያመለክት አይደለም፡፡ ይህ የሚናገረው ሙሴ ለእግዚአብሔር ያቀረበውን ዳቦ ነው፡፡

እነዚህን ሁሉ ለአሮንና ለልጆቹ በአጃቸው ሰጣቸው

እዚህ” እጆች” መላውን ሰው ያመለክታል፡፡ አማራጭ ትርጉም (አት)፤ “ሁሉንም ለአሮንና ለልጆቹ ሰጠው” (See Synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ እናም ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዜይቤያዊ አነጋገር ወይም ሥዕላዊ መግለጫ ይመልከቱ)::

የሚወዘወዝ መሥዋዕት አድርገው በእግዚአብሔር ፊት ወዘወዙት

አሮንና ልጆቹ መሥዋዕት እንዳቀረቡ የሚናገር ነው፡፡ የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉሙ ግልጽ ሊሆን ይችላል:: አት ፤ “እነርሱም በእግዚአብሔር ፊት እንደመወዘወዝ መሥዋዕት ወዘወዙት”:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ወዘወዙት

ይህ መሥዋዕቱ ለእግዚአብሔር የሚቀርብበት ምልክታዊ ድርጊት ነው፡፡ (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

Leviticus 8:28

ሙሴ እነዚህን ተቀበለ

እዚህ “እነዚህ” ሥቡን ወርቹንና ዳቦዎች በአጠቃላይ ያመለክታል::

ከእጃቸው

እዚህ “እጆች” መላውን ሰው ያመለክታሉ:: አት፤ “ከአሮንና ልጆቹ” (See Synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ እናም ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዜይቤያዊ አነጋገር ወይም ሥዕላዊ መግለጫ ይመልከቱ):: የቅድስና ወይም የመለየት መሥዋዕት ናቸው:: አሮንና ልጆቹን ለእግዚአብሔር አገልግሎት የሚለዩ መሥዋዕቶች ናቸው::

ለእግዚአብሔር በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት (ተሻጋሪ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመለከቱ)::

ሽታው ደስ የሚያሰኝ

እግዚአብሔር መሥዋዕትን በማቅረብ በቅንነት በሚያመልከው ሰው እንደሚደሰት በሚቃጠል መሥዋዕት ሽታ እንደተደሰተ ተደርጐ ተገልጾአል:: በዘሌዋዊያን 1:9 የዚህ ተመሳሳይ ሀረግ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::(ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ፍርምባ

ከአንገት በታች ያለ የእንስሳ የፊት አካል ነው::

ክህነት

አንድን ሰው ካህን የማድረግ ሥርዓታዊ በዓል ነው::

Leviticus 8:31

የመሥዋዕት መሶብ

አሮንና ልጆቹ በሚቀደሱበት ጊዜ መሥዋዕቶችን የያዘው መሶብ ማለት ነው፡፡ አት፤ “መሶቡ”

ብዬ በታዘዝሁት መሠረት “አሮንና ልጆቹ ይብሉት” ይህም ጥቅስ በጥቅስ ውስጥ ይዞአል ቀጥታ ጥቅስ እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ

ይችላል:: አት: “እንዲታደርጉ እንዳዘዝሁት” (ጥቅሶችን በጥቅሶች ውስጥ እና ቀጥታና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

የክህነት መቀበያችሁ ሰዓት እስከሚፈጸምበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ የክህነት ቀናት እስኪፈጽሙ፤ (ድረስ ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮች ይመልከቱ) ክህነት ይህ አንድን ሰው ካህን የማድረግ ሥርዓታዊ በዓል ነው በዘሌዋዊያን 8:29 ይህን እንዴት እንደተረጐው ይመልከቱ

Leviticus 8:34

መደረግ ያለበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ እኛ ማድረግ ያለብን (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ለእናንተ ማስተሠሪያ

“ሥርየት” የሚለው ረቂቅ ስም እንደ ግሥ ሊገለጽ ይችላል:: አት፤ “ኃጢአታችሁን ለማስተሠርየት” (ረቂቅ ስሞችን ይመልከቱ)

ያዘዝሁት ይህ ነው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እርሱ ያዘዘኝ ይህ ነው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)


Chapter 9

1 በስምንተኛው ቀን ሙሴ አሮንንና ልጆቹን እንዲሁም የእስራኤልን ሽማግሌዎች ጠራ፡፡ 2 አሮንን እንዲህ አለው፣ “ለኃጢአት መስዋዕት ከመንጋው እምቦሳ እና ነውር የሌለበትን አውራ በግ ወስደህ በያህዌ ፊት ሰዋቸው፡፡ 3 እስራኤል ሰዎች እንዲህ ባላቸው፣ ‘ለኃጢአት መስዋዕት ወንድ ፍየል ውሰድ እንደዚሁም ነውር የሌለባቸው የአንድ አመት እምቦሳና ጠቦት ለሚቃጠል መስዋዓት ውሰድ፤ 4 እንዲሁም በያህዌ ፊት የሰላም መስዋት ለመስዋዕት አንድ በሬና አንድ አውራ በግ ውሰድ፣ በዘይት የተለወሰ የእህል ቁርባንም አቅርብ፣ ምክንያቱም ዛሬ ያህዌ ይገለጥላችኋል፡፡” 5 ስለዚህም ሙሴ ያዘዘውን ሁሉ ወደ መገናኛው ድንኳን አመጡ፣ የእስራኤል ጉባኤም ሁሉ ቀርበው በያህዌ ፊት ቆሙ፡፡ 6 ከዚያም ሙሴ እንዲህ አለ፣ “ያህዌ እንድታደርጉት ያዘዘው ይህንን ነው፣ስለዚህም ክብሩ ይገለጥላችኋል፡፡” 7 ሙሴ አሮንን እንዲህ አለው፣ “ወደ መዊያው ቀርበህ የኃጢአት መስዋዕትህንና የሚቃጠል መስዋዕትህን አቅርብ፣ ደግሞም ያህዌ እንዳዘዘው ለራስህና ለህዝቡ አስተስርይ፣ ለህዝቡ ማስተስረያ ለማቅረብ መስዋዕቱን ሰዋ፡፡” 8ስለዚህም አሮን ወደ መሰዊያው ቀርቦ ለራሱ የሆነውን መስዋዕት ለኃጢአት መስዋዕት እምቦሳውን አረደ፡፡ 8 ስለዚህም አሮን ወደ መሰዊያው ቀርቦ ለራሱ የሆነውን መስዋዕት ለኃጢአት መስዋዕት እምቦሳውን አረደ፡፡ 9 የአሮን ልጆቸ ደሙን አቀረቡለት፣ እርሱም ጣቱን ደሙ ውስጥ እየነከረ በመሰዊያው ቀንዶች ውስጥ ጨመረ፤ ከዚያም በመሰዊያው ስር ደሙን አፈሰሰ፡፡ 10 ሆኖም ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው ስቡን፣ ኩላሊቶቹን እና በመሰዊያው ላይ የጉበቱን ሽፋን የኃጢአት መስዋዕት አድርጎ አቃጠላቸው፡፡ 11 ስጋውንና ቆዳውን ከሰፈር ውጭ አቃጠለው፡፡ 12 አሮን የሚቃጠለውን መስዋዕት አረደ፣ ልጆቹ በመሰዊያው ዙሪያ የሚረጨውን ደም ሰጡት፡፡ 13 ከዚያ የሚቃጠለውን መስዋዕት ከከብቱ ራስ ጋር እየቆራረጡ ሰጡት፣ እርሱም በመሰዊያው ላይ አቃጠለው፡፡ 14 የሆድ ዕቃዎቹንና እግሮቹን አጥቦ በመሰዊያው ላይ በሚቃጠል መስዋዕቱ ላይ አቃጠላቸው፡፡ 15 አሮን አንድ ፍየል የህዝቡን መስዋዕት አቀረበ፣ ከዚያ ለኃጢአታቸው መስዋዕት አድርጎ አረደው፤ በመጀመሪያው ፍየል ላይ እንዳደረገው ሁሉ ለኃጢአት መስዋዕትነት ሰዋው፡፡ 16 ያህዌ እንዳዘዘው የሚቃጠል መስዋዕቱን አቅርቦ ሰዋው፡፡ 17 የእህል ቁርባኑን፣ ከእህል ቁርባኑ እፍኝ ሙሉ ወስዶ ከማለዳው የሚቃጠል መስዋዕት ጋር በመሰዊያው ላይ አቃጠለው፡ 18 እንዲሁም ለህዝቡ የሰላም መስዋዕት የሆነውን መስዋዕት በሬውንና አውራ በጉን አረደ፡፡ የአሮን ልጆች በመሰዊያው ዙሪያ የሚረጨውን ደሙን ሰጡት፡፡ 19 ሆኖም፣ የበሬውንና የአውራ በጉን ስብ፣ ላቱን፣ ሆድ ዕቃውን ክፍሎች የሸፈነውን ስብ፣ ኩላሊቶቹን፣ የጉበቱን ሽፋን 20 እነዚህን በፍርምባው ላይ አደረጉ፣ ከዚያም አሮን ሙሴ ባዘዘው መሰረት ስቡን በመሰዊያው ላይ አቃጠለው፡፡ 21 አሮን ፍርምባውንና የቀኝ ወርቹን መስዋዕት አድርጎ በያህዌ ፊት ይወዝስዘውና እነዚህን ለያህዌ ያቅርብ፡፡ 22 ከዚያ አሮን አጆቹን ወደ ህዝቡ አንስቶ ይባርካቸው፤ ቀጥሎ የኃጢአት መስዋዕቱን፣ የሚቃጠል መስዋዕቱንና የሰላም መስዋዕቱን አቅርቦ ይወርዳል፡፡ 23 ሙሴና አሮን ወደ መገናኛው ድንኳን ይሂዱ፣ ከዚያ ተመልሰው ይውጡና ህዝቡን ይባርኩ፣ እናም የያህዌ ክብር ለህዝቡ ሁሉ ይገለጣል፡፡ 24 ከያህዌ ዘንድ እሳት ወጥቶ የሚቃጠል መስዋዕቱንና በመሰዊያው ላይ ያለውን ስብ ሁሉ በላ፡፡ ህዝቡ ሁሉ ይህንን ባዩ ጊዜ ጮኸው በፊታቸው ተደፉ፡፡



Leviticus 9:1

በስምንተኛውም ቀን

ስምንተኛ የሚለው ቃል ተራ ቁጥር ስምንት ነው:: (ተራ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር መገኘት”

Leviticus 9:3

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል::

እስራኤላዊያንንም እንዲህ በላቸው አንድ አውራ ፍየል ውሰዱ … ስለራሳችሁም ቁሙ

ሙሴ ለአሮን መናገር ቀጠለ:: ይህም በጥቅስ ውስጥ የሚገኝ ጥቅስ ነው:: ቀጥተኛ ጥቅስ እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል:: አት “አንድ አውራ ፍየል ይዘው….ለሕዝቡ ሁሉ እንዲያቀርቡ እስራኤላዊያንን ንገራቸው:: (ጥቅሶችን በጥቅሶች እና ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

የአንድ ዓመት ዕድሜ

“የአሥራ ሁለት ወር ዕድሜ”

በእግዚአብሔር ፊት ለመሥዋዕት

“ለእግዚአብሔር ለመሠዋት”

Leviticus 9:6

እናንተ እንዲታደርጉት እግዚአብሔር ያዘዛችሁ

እዚህ እናንተ የእስራኤልን ሕዝብ ያመለክታል (See forms of you/ሁለተኛ ሰው አገላለጽ አይነቶችን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔር ክብር ይገለጥላችሁ ዘንድ

እዚህ “ክብር” የእግዚአብሔርን መገለጥ ያመለክታል:: አት “እርሱ የክብሩ መገኘት ይገልጥለችሁ/ያሳያችሁ ዘንድ” (See Mentonymy/ተመሣሣይ ትርጉም የያዙ አባባሎች ዜይቤያዊ ንግግር ይመልከቱ)

ለራስህና ለሕዝቡም አስተሰርይ…ሊታስተሰርይላቸው ለሕዝቡ መሥዋዕት አቅርብ

እነዚህ ሁለት የተለያዩ መሥዋዕቶች ናቸው:: የመጀመሪያው የልቀ ካህኑን ኃጢአቶች ለማስተሠርየት ነው:: ሊቀ ካህኑ ኃጢአቶችን ሲፈጽም ሕዝቡን በደለኛ ያደርጋል:: ዘሌዋዊያን 4:3 ይመልከቱ:: ሁለተኛው ሕዝቡ የሠራቸውን ኃጢአት ለማስተሠርየት ነው::

Leviticus 9:8

የአሮን ልጆች ደሙን አቀረቡለት

ይህ ከእንስሳው እንደወጣ ደሙን የአሮን ልጆች በሳህን እንደያዙት ይገልጻል፡፡ የዐረፍተ ነገሩ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል (ግምታዊ እውቀት እና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የመሠዊያው ቀንዶች

ይህ የመሠዊያውን ማዕዘናት ያመለክታል እንደ በሬ ቀንዶች መልክ የተቀረጹ ናቸው፡፡ በዘሌዋዊያን 4፡7 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

በመሠዊያው ግርጌ

“ከመሠዊያው በታች”

Leviticus 9:10

እርሱ በእሳት አቃጠለው

“አሮን በእሳት አቃጠለው”

ኩላልቶች ጉበት

በዘሌዋዊያን 3፡4 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

ቁርበቱን

ይህ የቤት እንስሳ ቆዳ ወይም ሽፋን ነው:: በዘሌዋዊያን 7: 8 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Leviticus 9:12

ልጆቹ ደሙን አቀበሉት

ከእንስሳው እንደወጣ ልጆቹ ደሙን እንደያዙት የሚያመለክት ነው:: የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀት እና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የሆድ ዕቃዎች

የውስጥ ክፍሎች ሆድንና አንጀቶችን ነው፡፡ በዘሌዋዊያ 1፡9 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

Leviticus 9:15

የመጀመሪያው ፍየል

“መጀመሪያ” የሚለው ቃል ለተራ ቁጥር አንድ ነው:: አት “ለራሱ መሥዋዕት የሚያቀርበው ፍየል” (ተራ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ጧት ጧት ከሚቀርበው መሥዋዕት ተጨማሪ

ይህ የየዕለቱን የመጀመሪያ መሥዋዕት ያመለክታል፡፡ ካህኑ ከማንኛውም መሥዋዕት በፊት በማለዳ ይህን የሚቃጠል መሥዋዕት ማቅረብ አለበት፡፡ የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ (ግምታዊ እውቀት እና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 9:18

እርሱ ዐረደ

“አሮን ዐረደ”

የአሮን ልጆችም ደሙን አመጡለት

ይህም ደሙ በሳህኑ እንደነገበር ያመለክታል፤ የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ::

የሆድ ዕቃዎች

ይህ ሆድና አንጀቶችን ነው፡፡ ይህን በዘሌዋዊያን 1፡9 እንዴት እንደረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ኩላሊቶችና ጉበት

በዘሌዋዊያ 3፡4 እነዚህን ቃላት አንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

Leviticus 9:20

እነርሱ ክፍሎችን ወሰዱ

የአሮን ልጆች ክፍሎችን ወሰዱ

እነዚህን አስቀመጡ

“እነዚህ” የሚለው ቃል ቀድም ተብለው የተገለጹ ሥብንና የሆድ ዕቃዎችን ያመለክታል::

ፍርምባዎች

ከአንገት በታች የሚገኝ የእንስሳ ፊተኛ አካል ነው፡፡ በዘሌዋዊያን 7፡3ዐ ይህን እንዴት አንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ቀኝ ወርች

ከጉልበት በላይ የሚገኝ የእግር አካል ነው፡፡ በዘሌዋዊያን 7፡32 ይህን እንዴት እንደተዘጐሙ ይመልከቱ፡፡

በእግዚአብሔር ፊት

“ለእግዚአብሔር”

Leviticus 9:22

ካቀረበ በኋላ ወረደ

“ካቀረበ በኋላ ወረደ” የሚለው ሀረግ የተጠቀመበት መሠዊያው ሕዝቡ ከቆመበት ቦታ ከፍ ብሎ ስለሚገኝ ነው::

የእግዚአብሔርም ክብር ለሕዝቡ ተገለጠ

እዚህ “ክብር” የእግዚአብሔርን መገኘት ይወክላል:: አት፤ እግዚአብሔርም የመገኘቱን ክብር ለሁሉም ሕዝብ አሳየ:: (See Metonymy/ /ተመሣሣይ ትርጉም የያዙ አባባሎች ዜይቤያዊ ንግግር ይመልከቱ)

እሳት ከእግዚአብሔር ዘንድ ወጥቶ በላው

“የሚበላውን እሳት እግዚአብሔር ላከ”

የሚቃጠለውን መሥዋዕት በላ

እሳቱ መሥዋዕቱን ሙሉ በሙሉ ያቃጠለው እሳቱ የሚቃጠለውን መሥዋዕት እንደበላ ወይም እንዳቃጠለ ተነግሮአል፡፡ (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በግምባራቸው ተደፉ

“በግምባራቸው ወደ መሬት አጐነበሡ” ይህ የማክበርና ክብር መስጠት ምልክት ነው:: (ምልክታዊ ድርጊቶችን ይመልከቱ)


Chapter 10

1 የአሮን ልጆች ናዳብና አብዩድ እያንዳንዳቸው ጥናዎቻቸውን ወስደው እሳት አደረጉበት ከዚያም ዕጣን ጨመሩበት፡፡ ከዚያ በያህዌ ፊት እርሱ እንዲያቀርቡ ያላዘዛቸውን ያልተፈቀደ ዕሳት አቀረቡ፡፡ 2 ስለዚህም ከያህዌ ዘንድ እሳት ወጥታ በላቻቸው፣ እነርሱም በያህዌ ፊት ሞቱ፡፡ 3 ከዚያም ሙሴ አሮንን፣ “ያህዌ ‘ወደ እኔ በሚቀርቡ ላይ ቅድስናዬን እገልጻለሁ፡፡ በሰዎች ሁሉ ፊት እከብራለሁ’ ሲል ይህን ማለቱ ነው” አለው፡፡ አሮንም ምንም አልመለሰም፡፡ 4 ሙሴ የአሮን አጎት የሆነውን የዑዝኤልን ልጆች ሚሳኤልንና ኤልጻፋንን ጠርቶ እንዲህ አላቸው፣ “ወደዚህ ኑና ከመቅደሱ ደጃፍ ወንድሞቻችሁን ተሸክማችሁ ከሰፈር አውጣቸው፡፡” 5 ስለዚህም ሙሴ እንዳዘዘው ቀርበው የክህነት ቀሚሳቸውን እንደለበሱ ተሸክመው ከሰፈር አወጧቸው፡፡ 6 ከዚያም ሙሴ ለአሮንና ለልጆቹ ለአልአዛርና ለኢታምር እንዲህ አላቸው፣ “እንዳትቀሰፉ ፀጉራችሁን አትንጩ፣ ልብሳችሁንም አትቅደዱ፣ ያህዌ በህዝቡ ላይ ሁሉ እንዳይቆጣ ተጠንቀቁ፡፡ ነገር ግን ቤተዘመዶቻችሁና መላው የእስራኤል ቤት የያህዌ እሳት ለበላቻቸው ያልቅሱ፡፡ 7 እናንተ ግን ከመገናኛው ድንኳን ደጃፍ አትለፉ፣ የያህዌ የቅባት ዘይት በእናንተ ላይ ነውና ትሞታላችሁ፡፡ ስለዚህም ሙሴ እንዳዘዘው አደረጉ፡፡ 8 ያህዌ አሮንን እንዲህ አለው፣ 9 “አንተ፣ ወይም ከአንተ ጋር የሚሆኑ ልጆችህ ወደ መገናኛው ድንኳን ስትገቡ እንዳትሞቱ ወይን ጠጅ ወይም የሚያሰክር መጠጥ አትጠጡ፡፡ ይህ በትውልዳችሁ ሁሉ ቋሚ ስርዓት ይሆናል፣ 10 ቅዱስ በሆነውና ተራ በሆነው መሃል ለመለየት፣ ንጹህ በሆነውና ንጹህ ባልሆነው መሃል ለመለየት፣ 11 ለእስራኤል ህዝብ ሁሉ በሙሴ በኩል ያህዌ ያዘዘውን ስርዓት ሁሉ አስተምሩ፡፡” 12 ሙሴ ለአሮንና ለተረፉት ልጆቹ ለአልአዛርና ለኢታምርን እንዲህ አላቸው፣ “በእሳት ለያህዌ ከቀረበው የእህል ቁርባን የተረፈውን መስዋዕት ውሰድ፣ እጅግ ቅዱስ ነውና እርሾ ሳይገባበት ከመሰዊያው አጠገብ ብሉት፡፡ 13 በተቀደሰው ስፍራ ብሉት፣ ምክንያቱም በእሳት ለያህዌ ከቀረበው መስዋዕት ይህ የአንተና የልጆችህ ድርሻ ነው፣ እንድነግርህ የታዘዝኩት ይህንን ነው፡፡ 14 ለመስዋዕት የተወዘወዘውን ፍርምባና ለያህዌ የቀረበውን ወርች እግዚአብሔር ደስ በሚሰኝበት በተቀደሰው ስፍራ ብሉት፡፡ እነዚህን ድርዎቻችሁን አንተ፣ እንዲሁም ወንዶችና ሴቶች ልጆች ብሉት፣ እነዚህ የእስራኤል ህዝብ ከሚያቀርበው የህብረት መስዋዕት የአንተና የልጆችህ ድርሻ ሆነው ተሰጥተዋል፡፡ 15 ለያህዌ መስዋዕት ሆኖ የቀረበውን ወርች እና መስዋዕት ሆኖ የተወዘወዘውን ፍርምባ በእሳት ከተዘጋጀው የስብ መስዋዕቶች ጋር ከፍ አድርገው ለመወዘወዝና ለያህዌ መስዋዕት ለማድረግ በአንድነት ያቅርቧቸው፡፡ ይህም ያህዌ እንዳዘዘው ለዘለዓለም የአንተና የልጆችህ ድርሻ ይሆናል፡፡” 16 ከዚያ ሙሴ ለኃጢአት መስዋዕት ስለሚሆነው ፍየል ጠየቀ፣እናም በእሳት እንደተቃጠለ አወቀ፡፡ ስለዚህም በአልአዛርና በኢታምር በተቀሩትም የአሮን ልጆች ላይ ተቆጣ፤ እንዲህም አላቸው፣ 17 “ይህ የኃጢአት መስዋዕት እጅግ የተቀደሰ ሆኖ ሳለና የጉባኤውን በደል በእረሱ ፊት እንድታስወግዱበትና ኃጢአታቸውንም እንድታስተረዩላቸው ሰጥቷችሁ ሳለ ስለምን በቤተ አምልኮው ስፍራ አልበላችሁትም? 18 ተመልከቱ፣ ደሙ ወደ ቤተመቅደስ ውስጥ አልመጣም፤ እንዳዘዝኳችሁ በቤተ መቅደሱ አካባቢ ለትበሉት ይገባ ነበር፡፡” 19 ከዚያም አሮን ለሙሴ እንደህ ሲል መለሰለት፣ “እነሆ፣ ዛሬ የኃጢአት መስዋዕታቸውን እና የሚቃጠል መስዋዕታቸውን በያህዌ ፊት አቀርቡ፣ እናም ይህ ነገር በእኔ ላይ ደርሷል፡፡ ዛሬ እኔ የኃጢአት መስዋዕቱን ብበላ ኖሮ ይህ በያህዌ ፊት ደስ ያሰኝ ነበርን?” 20 ሙሴ ያንን ሲሰማ መልሱ አረካው፡፡



Leviticus 10:1

ናዳብና አብዩድ

እንዚህ የአሮን ልጆች ስሞች ናቸው

ጥና

ካህናት ፍምን ወይም እጣንን የሚሸከሙበት ጐድጓዳ የብረት መያዣ ነው

እሳት ጨመሩ

“የሚያቃጥል ፍም ጨመሩ”

እርሱ ያለዘዛቸውን ያልተፈቀደውን እሳት በእግዚአብሔር ፊት አቀረቡ

“እርሱ እንዲያቀርቡ ባዘዛቸው መንገድ ስላልሆነ እግዚአብሔር መሥዋዕታቸውን አላጸናም/አለፈቀደም”

በእግዚአብሔር ፊት ያልተፈቀደ እሳት

“ያልተፈቀደ እሳት ለእግዝአብሔር”

ከዚህም የተነሣ እሳት ከእግዚአብሔር ዘንድ ወጥቶ

“ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔር እሳት ላከ”

ከእግዚአብሔር ፊት ወጥቶ

“ከእግዚአብሔር ወጥቶ”

በላቸው

ሙሉ በሙሉ እሳቱ ሰዎችን ያቃጠለው እሳቱ እንደበላቸው ወይም ሙሉ በሙሉ እንዳቃጠላቸው ተገልጾአል፡፡ (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በእግዚአብሔርም ፊት ሞቱ

“በእግዚአብሔር መገኘት ሞቱ”

Leviticus 10:3

እግዚአብሔርም ሲናገር ያለው ይህ ነው ፤ቅድስናዬን በሕዝቡም ሁሉ ፊት እገልጣለሁ፡፡

ይህ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ ይዞአል ቀጥተኛ ጥቅስ እንደተዘዋዋሪ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፤ “ወደ እኔ በሚቀርቡት …ቅድስናዬን አግልጣለሁ እናም በሕዝቡ.. እከብራለሁ ባለ ጊዜ እግዚአብሔር ይናገር የነበረው ይህ ነው” (ጥቅሶችን በጥቅሶች ውስጥ እናም ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ጥቅሶችን ይመልከቱ)

ወደ እኔ በሚቀርቡት መካከል ቅድስናዬን እገልጣለሁ

ወደ እኔ በሚቀርቡት የሚለው ሀረግ እግዚአብሔርን የሚያገለግሉ ካህናትን ያመለክታል፡፡ ወደ እኔ ለሚቀርቡ ቅዱስ እንደሆንሁ እገልጣለሁ ወይም ሊያገለግሉት ወደ እኔ የሚቀርቡ ቅዱስ እንደሆንሁ ይወቁኝ

በሕዝቡም ሁሉ ፊት እከብራለሁ

እግዚአብሔር ከተናገረው ሁለተኛው ክፍል እግዚአብሔርን ለማገልገል ስለሚቀርቡ ካህናት ይመለከታል፡ ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “በሕዝብ ሁሉ ፊት ሊያከብሩኝ ይገባል” ወይም “በሕዝብ ሁሉ ፊት ከፍ ሊያደርጉኝ የገባል”፡፡

ሚሳኤል… ኤልጻፋ… ዑዝኤል

እንዚህ የሰው ስሞች ናቸው:: (የሰው ስሞች ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ወንድሞቻችሁ

እነዚህ በሥጋ ወንድሞች ናቸው ማለት አይደለም፡፡ እዚህ “ወንድሞች” ዘመዳሞች; የአጐት ወይም የአክስት ልጆች

Leviticus 10:5

እነርሱም መጥተው

ሚሳኤልና ኤልጻፋን መጥተው

ሟቾቹ የክህነት ልብሳቸውን እንደለበሱ ተሸክመው

የናዳብና አብዩድ ሙት አካል በክህነት ልብሶቻቸው እንዳለ ተሸክመው

አልአዛር…ኢታምር

እነዚህ የአሮን ልጆች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ጸጉሮቻችሁን አትንጩ ልብሶቻችሁን አትቅደዱ

አሮንና ልጆቹ ምንም ዓይነት ውጫዊ ሃዘን ወይም ትካዜ እንዳያሳዩ እግዚአብሔር ይናገራቸዋል፡፡ (ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ)

ስለዚህ እንዳትሞቱ

ከዚህ የተነሣ እንዳትሞቱ

በእስራኤል ጉባኤ ላይ ቁጣ እንዳይመጣ

እዚህ “ጉባኤ” መላውን የእስራኤል ጉባዔ እንጂ የቡድን መሪዎችን አይደለም (See Synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ እናም ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዜይቤያዊ አነጋገር ወይም ሥዕላዊ መግለጫ ይመልከቱ)::

መላው ቤተ እስራኤል

እዚህ “ቤት” ሰዎችን ይወክላል:: አት : “መላው የእስራኤል ሕዝብ”

እግዚአብሔር በእሳት ስላቃጠላቸው ሰዎች

“እግዚአብሔር በእሳት ስላጠፋቸው ሰዎች”

Leviticus 10:8

ይህም

እዚህ “ይህ” ወደ ኋላ መለስ ብሎ ካህናት ወደ መገናኛው ድንኳን በሚገቡበት ጊዜ ወይን ወይም ጠንካራ መጠጥ እንዳይጠጡ የታዘዙትን የሚያመለክት ነው::

በልጅ ልጆቻችሁ ዘንድ የሚጠበቅ ዘላለማዊ ሥርዓት ነው:: በዘሌዋዊያን 3፡17 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::ለመለየት

በዚህ አድስ ዐረፍተ ነገር መጀመር ይቻላል:: “መለየት ይችሉ ዘንድ ይህን ያድርጉ”

በተቀደሰውና ባልተቀደሰው መካከል

“የተቀደሰ” እና “ያልተቀደሰ” ቅጽል ሥሞች እንደ ቅጽል ግሥ ሊገለጹ ይችላሉ:: አት: “ቅዱስ በሆነውና ቅዱስ ባልሆነው ወይም ለእግዚአብሔር በተለየውና በተራው” (ቅጽል ሥሞችን ይመልከቱ)

በርኩሱና ንጹሑ መካከል

“ርኩሱ” እና “ንጹሑ” ቅጽል ሥሞች እንደ ቅጽል ግሥ ሊገለጹ ይችላሉ:: አት: “ርኩሰ በሆነውና ንጹህ በሆነው በካከል ወይም እግዚአብሔር በማይቀበለውና በሚቀበው መካከል” (ቅጽል ሥሞችን ይመልከቱ)

ርኩስ

እግዚአብሔር እንዲነካ ያልፈለገው ሰው ወይም አንድ ነገር በአካል ርኩስ ተደርጐ ተገልጾአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ንጹህ

እግዚአብሔር እንዲነካ የፈለገው ሰው ወይም አንድ ነገር በአካል ንጹህ ተደርጐ ተገልጾአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 10:12

በእሳት ለእግዚአብሔር የሚቀርበው ቁርባን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ለእግዚአብሔር የሚቀርብ የሚቃጠል መሥዋዕት”(ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮች ይመልከቱ)

ይህ እጅግ ቅዱስ ስለሆነ

የእህል ቁርባኑ እጅግ ቅዱስ ስለሆነ ይህን እንዲትናገር ያዘዝሁት ነው:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ይህም እንዲናገር እግዚአብሔር ያዘዘኝ ነው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮችን ይመልከቱ)

Leviticus 10:14

የተወዘወዘውን ፍርምባና ለእግዚአብሔር የቀረበውን ወርች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “ለእግዚአብሔር የተወዘወዘውና የቀረበው ፍርምባና ወርች” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮችን ይመልከቱ)

ፍርምባ

ከአንገት በታች የሚገኝ የእንስሳ ፊት አካል ክፍል ነው፡፡

ወርች

ከጉልበት በላይ የሚገኝ ላይኛ የእግር አካል ክፍል ነው፡፡

ንጹህ በሆነ ሥፍራ

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ጥቅም ተገቢ ሥፍራ በአካል ንጹህ ተብሎ ተገልጾአል፡፡ (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እነዚህ ለእናንተ የተመደቡ ድርሻ ናቸው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “እግዚአብሔር እነዚህን ለእናንተ ድርሻ አድርጐ ስጥቶአችኋል” (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮች ይመልከቱ)

አንተ እና ወንዶችና ሴቶች ልጆችህ

እዚህ “አንተ” አሮንን ያመለክታል:: (ሁለተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

ለአንተና ለልጆችህ ለዘላለም የተመደበ ድርሻ ይሆናል

ድርሻው ለአሮንና ለልጆቹ ተደርጐ እንደተገለጸ ይተርጉሙ፡፡ አት፡ “ይህ ድርሻ ሁልጊዜ ለአንተና ለልጆችህ ይሆናል” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 10:16

ተቃጥሎአል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “ካህናት ሁሉንም አቃጥለዋል”

አልዓዛርና ኢታምር

እነዚህን ስሞች በዘሌዋዊያን 1ዐ:6 እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ለምን… በፊቱ አልበላችሁም?

ሙሴም በጥያቄ መልክ አልዓዛርንና ኢታምርን ይቆጣቸዋል፡፡ ይህ ጥያቄያዊ አገላለጽ በስድ ዐረፍተ ነገር ሊቀመጥ ይችላል፡፡ አት፡ በፊቱ መብላት የገባችሁ ነበር፡፡

እጅግ የተቀደሰ ነው

የኃጢአት መስዋዕት እጅግ የተቀደሰ ነው፡፡

የሕዝቡን ኃጢአት እንዲታስወግዱበት

እግዚአብሔር የእስራኤልን ኃጢአት ይቅር ማለቱ ኃጢአት እግዚአብሔር ከሕዝቡ ላይ የሚያስወግደው ነገር እንደሆነ ተገልጾአል፡፡ (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በፊቱ

በመገኘቱ

ደሙ አልገባም

ይህ በተሻጋሪ ግሥ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “እነርሱ ደሙን አላመጡም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዙ ዐረፍተ ነገሮችን ይመልከቱ)

Leviticus 10:19

እንዲህ ያለ ነገር ደረሰብኝ

አሮን ስለሞቱ ሁለት ልጆቹ ያውሳል

ይህ በእግዚአብሔር ፊት ደስ የሚያሰኝ ኖሮአልን?

እነዚህ መሥዋዕቶች በእግዚአብሔር ፊት በፍስሃና በደስታ መበላት አለባቸው፡፡ በልጆቹ ሞት ምክንያት ሀዘንተኛ ስለሆነ መሥዋዕቶችን ቢበላ እግዚአብሔር ደስተኛ እንደማይሆን ለማተኮር አሮን በጥያቄ መልክ ያስቀምጣል:: ይህም ጥያቄ በስድ ዐረፍተ ነገር መልክ ሊተረጐም ይችላል:: “በእርግጥ እግዚአብሔር አልተደሰተም ኖሮአል::” (See Rehtorical Question/ንግግራዊ ጥያቄ ይመልከቱ)


Chapter 11

1 ያህዌ ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፣ 2 “ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በሏቸው፣ ‘በምድር ላይ ከሚገኙ እንስሳት ሁሉ የምትመገቧቸው ህያዋን ነገሮች እነዚህ ናቸው፡፡ 3 የተሰነጠቀ ሰኮና ያላቸውንና የሚያመሰኩትን ትመገባላችሁ፡፡ 4 ሆኖም፣ የሚያመሰኩ ቢሆኑም ነገር ግን የተሰነጠቀ ሰኮና የሌላቸውን እንደ ግመል ያሉትን አትብሉ፤ምክንያቱም ያመሰኳሉ ነገር ግን ሰኮናው አልተሰነጠቀም፡፡ ስለዚህ ግመል ለእናንተ ንጹህ አይደለም፡፡ 5 እንዲሁም ሽኮኮ ያመሰኳል ነገር ግን የተሰነጠቀ ሰኮና የለውም፣ ይህም ለእናንተ ንጹህ አይደለም፡፡ 6 ጥንቸል ቢያመሰኳም የተሰነጠቀ ሰኮና ስለሌለው ለእናንተ ንጹህ አይደለም፡፡ 7 አሳማ የተሰነጠቀ ሰኮና ቢኖረውም፣ አያመሰኳም ስለዚህ ለእናንተ ንጹህ አይደለም፡፡ 8 የእነዚህን ስጋ ፈጽሞ አትብሉ፣ ጥንባቸውንም አትንኩ፡፡ እነርሱ ለእናንተ ንጹህ አይደሉም፡፡ 9 በውቂያኖስም ሆነ በባህር በውሃ ውስጥ ከሚኖሩ እንስሳት የምትበሏቸው ክንፍና ቅርፊት ያላቸው ናቸው፡፡ 10 ነገር ግን በውቂያኖስ ወይም በባህር የሚኖሩ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ህያዋን ፍጥረታት ሁሉ፣በውሃ ውስጥ የሚንቀሳቀሱትን ጨምሮ እንዲሁም በውሃ ውስጥ ያሉት እንዲህ ያሉ ህያዋን ፍጥረታት በሙሉ በእናንተ ዘንድ ጸያፍ ናቸው፡፡ 11 ጸያፍ ሊሆኑ ስለሚገባቸውም፣ ስጋቸውን ልትበሉ አይገባም፣ እንደዚሁም በድናቸውም ጸያፍ ነው፡፡ 12 በውሃ ውስጥ የሚኖሩ ቅርፊት የሌላቸው እንስሳት ሁሉ፣በእናንተ ዘንድ ጸያፍ ናቸው፡፡ 13 ልትጸየፏቸው የሚገቡና የማትበሏቸው ወፎች እነዚህ ናቸው፤ ንስር፣ ጥንብ አንሳ፣ 14 ጭላት፣ ማንኛውም አይነት የሎስ 15 ማንኛውም አይነት ቁራ፣ 16 የተለያ አይነት ጉጉት፣ የባህር ወፍ እና ማንኛውም ዐይነት ጭልፊት፡፡ 17 ትናንሽና ትላልቅ ጉጉቶችን ትጸየፋላችሁ፣ርኩምና ጋጋኖ፣ 18 የተለያዩ ጉጉቶች፣ ይብራ፣ 19 ሽመላ፣ ማናቸውም ዐይነት የውሃ ወፍ፣ ሳቢሳ፣ ጅንጁላቲ ወፍና የለሊት ወፍ፡፡ 20 በእግራቸው የሚራዱ ክንፍ ያላቸው በራሪ ነፍሳት በሙሉ በእናንተ ዘንድ አስጸያፊ ናቸው፡፡ 21 ሆኖም ግን ከእግራቸው በላይ በምድር ላይ የሚፈናጠሩበት አንጓ ያላቸውን ማናቸውንም የሚበሩ ነፍሳት መብላት ትችላላችሁ፡፡ 22 እንደዚሁም ደግሞ ማናቸውንም ዐይነት አንበጣ፣ ትልቅ የአንበጣ ዝርያ፣ ፌንጣና ዝንቢት መብላት ትችላላችሁ፡፡ 23 ነገር ግን አራት እግር ያላቸው የሚበሩ ነፍሳት ሁሉ በእናንተ ዘንድ የተጠሉ ናቸው፡፡ 24 ከእነዚህ እንስሳት ውስጥ የአንዱን በድን ብትነኩ እስከ ማታ ድረስ የረደሳችሁ ናችሁ፡፡ 25 ከእነዚህ የአንዱን በድን ያነሳ ማንም ሰው ልብሱን ይጠብ፣ እስከ ማታ ድረስ እርኩስ ነው፡፡ 26 ማንኛውም ሙሉ ለሙሉ ያልተሰነጠቀ ሰኮና ያለው እንስሳ ወይም የማያመሰኳ እንስሳ በእናንተ ዘንድ ጸያፍ ነው፡፡ እነዚህን የነካ ሁሉ ይረክሳል፡፡ 27 በአራት እግሩ ከሚራመድ እንስሳ መሃል በመዳፋቸው የሚሄዱ ሁሉ በእናንተ ዘንድ እርሱስ ናቸው፡፡ እንደነዚህ ያሉትን በድናቸውን የነካ እስከ ማታ እርኩስ ነው፡፡ 28 እንደነዚህ ያሉትን በድናቸውን ያነሳ ልብሱን ይጠብ እስከ ማታ ድረስ እርኩስ ይሆናል፡፡ እነዚህ እንስሳት በእናንተ ዘንድ እርኩስ ናቸው፡፡ 29 በምድር ላይ ከሚሳቡ እንስሳት መሃል፣ በእናንተ ዘንድ እርኩስ የሆኑት እነዚህ ናቸው፡ አቁስጣ፣ አይጥ፣ ማናቸውም አይነት እንሽላሊት 30 ትንሽ የቤት ላይ እንሽላሊት እና እስስት 31 ከሚሳቡ እንስሳት በእናንተ ዘንድ እርኩስ የሆኑት እነዚህ ናቸው፡፡ ከእነዚህ የሞቱትን አንዳቸውን የነካ ሰው እስከ ምሽት እርሱስ ይሆናል፡፡ 32 ከእነዚህ መሃል አንዱ ሞቶ በማናቸውም ከእንጨት፣ ከጨርቅ፣ ከቆዳ ወይም ከበርኖስ በተሰራ ነገር ላይ ቢወድቀቅ ያዕቃ እርኩስ ይሆናል፡፡ ዕቃው ምንም ይሁን ለምንም አይነት ተግባር ይዋል ውሃ ውስጥ ይነከር እስከ ምሽት ድረስ እርኩስ ነው፡፡ ከዚያ ንጹህ ይሆናል፡፡ 33 ንጹህ ያልሆነ እንስሳ የገባበት ወይም የነካው የሸክላ ማሰሮ እንዲሁም በውስጡ ያለው ነገር ሁሉ እርኩስ ይሆናል፤ ያንን ማሰሮ ሰባብረው፡፡ 34 ማናቸውም ለመበላት የተፈቀደ ምግብ፣ ንጹህ ካልሆነ ማሰሮ ውሃ ቢገባበት እርኩስ ይሆኖል፡፡ እንዲህ ካለው ማሰሮ ማንኛውም ነገር ቢጠጣ ያረክሳል፡፡ 35 እርኩስ ከሆነ እንስሳ በድን ማናቸውም አካሉ የወደቀበት ምድጃም ሆነ የማብሰያ ሸክላ እንዲሁም ማንኛውም ነገር ይረክሳል፡፡ ይሰባበር፡፡ እርኩስ ነው፣ በእናንተም ዘንድ የተጠላ ይሁን፡፡ 36 የመጠጥ ውሃ የሚገኝበት ምንጭ ወይም የውሃ ጉድጓድ እንዲህ ያሉ እንስሳት ቢገኙበትም ንጹህ ነው፡፡ ነገር ግን ማንም ሰው በውሃው ውስጥ የሚገኘውን እርኩስ የሆነውን በድን ቢነካ እርኩስ ይሆናል፡፡ 37 ንጹህ ያልሆነ እንስሳ በድን በዘር ላይ ቢወድቅ፣ እነዚያ ዘሮች የረከሱ ይሆናሉ፡፡ 38 ነገር ግን በዘሮቹ ላይ ውሃ ቢፈስ ንጹህ ያልሆነው እንስሳ በድን ማንኛውም አካል የተክል ዘሩ ላይ ቢወድቅ ዘሩ በእናንተ ዘንድ እርኩስ ይሆናል፡፡ 39 ለመበላት ከተፈቀደው እንስሳ አንዱ ቢሞት፣ በድኑን የነካው ሰው እስከ ምሽት እርኩስ ይሆናል፡፡ 40 ደግሞም እንዲህ ያለውን በድን ያነሳ ሰው ልብሱን ያጥባል፣ እስከ ምሽት ድረስ እርኩስ ይሆናል፡፡ 41 ማንኛውም በምድር ላይ የሚሳብ እንስሳ ጸያፍ ነው፤ አይበላም፡፡ 42 በሆዱ የሚሳብ እንስሳ ሁሉ፣ እና በአራቱም እግሮቹ የሚራመድ፣ወይም ማንኛውም ብዙ እግሮች ያሉት - በምድር የሚሳብ እንስሳን ሁሉ፣ አትብሉ፤ እነዚህ ጸያፍ ናቸው፡፡ 43 በደረቱ በሚሳብ ማናቸውም ህያው ፍጥረት ራሳችሁን አታርክሱ፤ እነዚህ እናንተን ያረክሳሉ፡፡ 44 እኔ አምላካችሁ ያህዌ ነኝ፡፡ በምድር በሚንቀሳቀስ በማናቸውም አይነት እንስሳ ራሳችሁን አታርክሱ፡፡ 45 እኔ አምላካችሁ እሆን ዘንድ ከግብጽ ምድር ያወጣኋችሁ ያህዌ ነኝ፡፡ ስለዚህ እኔ ቅዱስ እንደሆንኩ እናንተም ቅዱስ መሆን አለባችሁ፡፡ 46 ስለ እንስሳት፣ ስለ ወፎች፣ በውሃ ውስጥ ስለሚንቀሳቀሱ ማናቸውም ህያዋን ፍጥረታት፣ እንዲሁም በምድር ላይ ስለሚሳቡ ፍጥረታት ህጉ ይህ ነው፤ 47 ንጹህ ባልሆኑና ንጹህ በሆኑት መካከል ልዩነት ለመፍጠር፣ እና በሚበሉ ህያዋን ነገሮችና በማይበሉ ህያዋን ነገሮች መሃል ለመለየት ህጉ ይህ ነው፡፡’”



Leviticus 11:1

እንስሳት ሁሉ መካከል

በየብስ ሚኖሩ እንስሳት ሁሉ

Leviticus 11:3

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ እንዲበሏቸው የተፈቀደላቸውንና ያልተፈቀደላቸውን እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን ይናገራል::

ሰኮናው የተሰነጠቀው

ይህም ሰኮናው አንድ ከመሆን ይልቅ ለሁለት የተሰነጠቀውን ማለት ነው::

Leviticus 11:5

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ እንዲበሏቸው የተፈቀደላቸውንና ያልተፈቀደላቸውን እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገርን ቀጠለ::

ሽኮኮ

በድንጋማ ቦታዎች የሚኖር ትንሽ እንስሳ ነው፡፡ (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

በእናንተ ዘንድ ርኩስ ይሁን

እነዚህን እንስሳት ሕዝቡ እንዲበላ ተገቢ እንዳይደለ እግዚአብሔር ስለተናገረ በአካል ርኩስ ተብለው ተገልጸዋል፡፡

ጥንቸል

ሁልጊዜ በጉዳጓድ በመሬት ውስጥ የሚኖር ጆሮው ረጅም የሆነ እንስሳ ነው፡፡

ጥምባቸውንም አትንኩ

ሙት አካላቸውን/በድናቸውንም አትንኩ

Leviticus 11:9

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ እንዲበሏቸው የተፈቀደላቸውንና ያልተፈቀደላቸውን እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገርን ቀጠለ::

ክንፎች

በዉሃ ውስጥ እንዲንሣፈፍ የሚያደርጉ የዓሣ ስስና ጠፍጣፋ የአካል ክፍሎች ናቸው፡፡

ቅርፊቶች

የዓሣን አካል ቆዳ የሚሸፍኑ ትናንሽ ቅርፊቶች ናቸው፡፡

በባሕሮችና በወንዞች ውሃ ውስጥ የሚኖሩ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ሕይወት ያላቸው ፍጡሮች

በባሕሮችና በወንዞች ውሃ ውስጥ ከሚኖሩት ፍጡሮች ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው፡፡

በእናንተ ዘንድ እስጸያፊ ይሁኑ

እግዚአብሔር ሕዝቡ እነዚህን ፍጡሮች መብት እንዳይቀበሉና እንዲንቁ ያዝዛቸዋል፡፡ ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “እነዚህን ተጸየፉአቸው ወይም ሙሉ በሙሉ አትቀበሉአቸው:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 11:11

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ እንዲበሏቸው የተፈቀደላቸውንና ያልተፈቀደላቸውን እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገርን ቀጠለ::

በእናንተ ዘንድ አስጸያፊ ስለሆኑ

አስጸያፊ የተናቀ ወይም ያልተቀበለ ነገር ነው፡፡ ይህም ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “በእናንተ ዘንድ ስለሚትጸየፉ” ወይም “እናንተ ሙሉ በሙሉ ስላተቀበላችሁ”:: (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በድናቸውንም ትጸየፋላችሁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “የእነርሱን ሙት አካል ትጸየፋላችሁ” ወይም “የእነርሱን ሙት አካል አትንኩ” (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ ይመልከቱ)

በውሃ ውስጥ ማንኛውም ክንፍና ቅርፊት የሌለው

ክንፍና ቅርፊት የሌለው ማንኛውም በውሃ ውስጥ የሚኖር

በእናንተ ዘንድ አስጸያፊ ይሁን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት: “ተጸየፉት” ወይም “ሙሉ በሙሉ አትቀበሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 11:13

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ እንዲበሏቸው የተፈቀደላቸውንና ያልተፈቀደላቸውን እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገርን ቀጠለ::

ንሥር; ጥንብ አንሣ; ግልገል አንሣ; ጭልፊት ቁራ ሰጐን ጠለቋ በቋል

እነዚህ አእፋት በሌሊት የሚንቀሳቀሱ ወይም የሞቱ እንስሳትንና ጥንብ የሚመገቡ ናቸው፡፡ (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Leviticus 11:17

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ እንዲበሏቸው የተፈቀደላቸውንና ያልተፈቀደላቸውን እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገርን ቀጠለ::

ጉጉት ርኩም ጋጋኖ የውሃ ዶሮ ይብራ ስደተኛ አሞራ ሽመላ

እነዚህ አእዋፋት በተለይ በሌሊት የማይተኙና ጥንብና ትላትሎችን የሚመገቡ ናቸው የማይታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ::

ሰቢሳ

ትልቅ ወፍ

ጅንጅላቴ ወፍ

እነዚህ እንሽላሊቶችንና ጥንብ ነገር የሚመገቡ ወፎች ናቸው፡፡

የሌሊት ወፍ

የሌሊት ወፍ ወፍ ባትሆንም ክንፍ ስላለውና ስለሚበርር በዝርዝሩ ውስጥ ተካትቶአል፡፡ ጸጉራማ አካል ያለውና በሌሊት የማይተኛ ነው፡፡ ጥምብንና ትላትሎችን የሚመገብ ነው::

Leviticus 11:20

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ እንዲበሏቸው የተፈቀደላቸውንና ያልተፈቀደላቸውን እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገርን ቀጠለ::

ክንፍ ኖሮአቸው በአራት እግር የሚንቀሳቀሱ ነፍሳት ሁሉ በእናንተ ዘንድ አስጸያፊዎች ይሁኑ

“አስጸያፊ” የሚለው ቃል በግሥ ሃረግ ሊተረጐም ይችላል አት ክንፍ ኖሮአቸው አራት እግር ያሉአቸውን ነፍሳት ይጸየፉ፡፡ (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

በአራት እግር የሚንቀሳቀሱ ነፍሳት

እዚህ “አራት እግር” የሚለው ሀረግ በምድር የሚንቀሳቀሱ መሆናቸውንና እንደ አእዋፋት ከመሠሉ ሁለት እግር ካላቸው ከሚበርሩ ነፍሳት እንደሚለዩ የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው:: አት፡ “በምድር የሚንቀሳቀሱ ነፍሳት” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አንበጣ ፈንጣ ኩብኩባ

እነዚህ ዕጽዋት ተመጋቢና የሚፈናጠሩ ትናንሽ እንስሳት ናቸው፡፡ (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ባለአራት እግር የሚበርሩ ፍጥረታት ወይም ነፍሳት

“አራት እግር ያሉአቸው የሚበርሩ ፍጥረታት”

Leviticus 11:24

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ርኩስ አድርጐ መቁጠር ስላለባቸው እንስት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን ይናገራል::

ከእነዚህ እንስሳት የአንዳቸውን በድን ቢነኩ እስከ ማታ ድረስ ርኩስ ይሆናሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “የእነዚህን እንስሳት በድን አንዳቸውን ከነካችሁ ርኩስ ያደርጋችኋል” (ተሻጋሪ ግሥና የማይሻገር ግሥ የያዘውን ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ርኩስ ይሆናሉ

ከእነዚህ በድን እንስሳት አንዱን በመንካቱ ምክንያት ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ተቀባይነት ያጣው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎ ተገልጾአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እነዚህ እንስሳት

በሚቀጥሉት ጥቅሶች የተዘረዘሩ እንስሳትን ያመለክታል::

Leviticus 11:26

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ርኩስ አድርጐ መቁጠር ስላለባቸው እንስሳት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገር ይቀጥላል::

ማንኛውም እንስሳ….በእናንተ ዘንድ ርኩስ ይሁን

ሕዝቡ አንዲመገቡ ያልተገቡ እግዚአብሔር የተናገራቸው እነዚህ እንስሳት በአካል ርኩስ ተብለው ተገልጸዋል፡፡ (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሰኰናው የተሰነጠቀ

አንድ ድፍን በመሆን ፈንታ ሰኰናው ለሁለት የተሰነጠቀ ማለት ነው፡፡ በዘሌዋዊያን 11፡3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

የሚያመስኩ ወይም የሚያመነዥጉ

ይህ ምግብን ከሆድ እንደገና ወደ አፍ በማምጣት የሚያኝኩ እንስሳት ማለት ነው፡፡ በዘሌዋዊያን 11፡3 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

እነዚህን የሚነካ ሰው ሁሉ ይረክሳል

እነዚህን እንስሳት በመንካቱ ምክንያት ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባ ሰው በአካል ርኩስ ተደርጐ ተገልጾአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

መዳፍ

ሾህና ያላቸው እንስሳት መረገጫ አካል

እስከ ማታ

ጸሐይ እስክትጠልቅ

Leviticus 11:29

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ርኩስ አድርጐ መቁጠር ስላለባቸው እንስሳት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገር ይቀጥላል::

እነዚህ እንስሳት በእናንተ ዘንድ ርኩስ ናቸው

ሕዝቡ አንዲመገቡ ያልተገቡ እግዚአብሔር የተናገራቸው እነዚህ እንስሳት በአካል ርኩስ ተብለው ተገልጸዋል፡፡

ሙጭልጭላ

ወፎችንና ትናንሽ እንስሳትን የሚመገብ ቡኒ ጸጉር ያለው ትንሽ እንስሳ ነው

ዐይጥ እንሽላሊት ዔሊ ዐዞ ገበሎ አርጃኖ ዕስስት

እነዚህ አራት እግር ያላቸው የተለያዩ ተሳቢ እንስሳት ናቸው:: ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ::

አርጃኖ

በአሽዋ የማኖር እንሽላሊት ነው::

Leviticus 11:31

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ርኩስ አድርጐ መቁጠር ስላለባቸው እንስሳት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገር ይቀጥላል::

እነዚህ እንስሳት በእናንተ ዘንድ ርኩስ ናቸው

ሕዝቡ አንዲመገቡ ወይም እንዲነኩ ያልተገቡ እግዚአብሔር የተናገራቸው እነዚህ እንስሳት በአካል ርኩስ ተብለው ተገልጸዋል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እነዚህን የሚነካ ሁሉ ርኩስ ይሆናል

ከነዚህ እንስሳት በድን አንዱን በመንካቱ ምክንያት ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባ ሰው በአካሉ ርኩስ ተደርጐ ተገልጾአል:: (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እስከ ማታ

ጸሐይ እስክትጠልቅ

እነዚህ በእናንተ ዘንድ ርኩሳን ናቸው

ከነዚህ በድን እንስሳት አንዳቸው በመጣላቸው ምክንያት ሕዝቡ እንዲነኩአቸው ያልተገባ እግዚአብሔር የተናገረው ነገር በአካል ርኩስ ተደርጐ ተገልጾአል በውሃ ከታጠበ በኋላ ንጹህ ተደርጐ ተገልጾአል (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ከዚያም በኋላ ንጹህ ይሆናል

ከታጠበ በኋላ ሕዝቡ አንድነካ የተገባ እግዚአብሔር የተናገረው ነገር በአካል ንጹህ ተደርጐ ተገልጾአል፡፡

ማንኛውም የተጠቀመበት ዕቃ በውሃ ውስጥ ይደረግ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ “የተጠቀሙ ቢሆን በውሃ ይደረግ ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ”

Leviticus 11:34

ርኩስ

ርኩስ የሆነ ውሃ በላዩ ላይ በመፍሰሱ ምክንያት ሕዝቡ መብላት ያልተገባው ምግብ ርኩስ ተደርጐ ተነግሮአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

በድኖች

ሙት አካላት

ይሰበር

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ ይህን ይሰባብሩት ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ፡፡

Leviticus 11:36

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ርኩስ አድርጐ መቁጠር ስላለባቸው እንስሳት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገር ይቀጥላል::

ምንጭ ወይም የውሃ ማጠራቀሚያ

ከምንጭ ወይም ከውሃ ማጠራቀሚያ ሕዝቡ እንዲጠጣ የተፈቀደለት በአካል ንጹህ ተብሎ ተነግሮአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

በድን

እግዝአብሔር የተናገረው ሕዝቡ እንዲበላ ወይም እንዲነካ ያልተገባው የእንስሳ በድን በአካል ርኩስ ተብሎ ተገልጾአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ርኩስ

የእነዚህን እንስሳት በድን በመንካቱ ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባ ሰው በአካል ርኩስ ተደርጐ ተነግሮአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

የሚዘራ ዘር

ለመዝራት የሚያስቡት ዘር

ዘሩ ንጹህ እንደሆነ ይቆያል ….ዘሩ ርኩስ ይሆናል

ሕዝቡ እንዲዘራ የተገባው እግዚአብሔር የተናገረው ዘር ንጹህ ተደርጐ ሲገለጽ ያልተገባው ዘር ግን ርኩስ እንደሆነ ተነግሮአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ነገር ግን በዘሩ ላይ ውሃ ከፈሰሰበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል አት ነገር ግን በዘሩ ላይ ውሃ ከጨበሩበት ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ

Leviticus 11:39

በድኑን የሚነካ እስከማታ ድረስ ርኩስ ይሆናል

የእንስሳ በድን በመንካቱ ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባ ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያል አነጋገር ይመልከቱ)

እስከ ማታ

ጸሐይ እስኪጠልቅ

Leviticus 11:41

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ርኩስ አድርጐ መቁጠር ስላለባቸው እንስሳት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገር ይቀጥላል::

ጸያፍ ነው

ተሻጋሪ ግሥ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: “ተጸየፉት” ወይም “አትቀበሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ ይመልከቱ)

ይህ አይበላ

ተሻጋሪ ግሥ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: “ይህን አይብሉ”:: (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ ይመልከቱ)

እነዚህ ጸያፍ ናቸው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: “እነዚህን ተጸየፉአቸው” ወይም “ እነዚህን አትቀበሉአቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 11:43

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ርኩስ አድርጐ መቁጠር ስላለባቸው እንስሳት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገር ይቀጥላል::

በእነዚህ…ራሳችሁን አስጸያፊ አታድርጉ፤ በእነርሱ ራሳችሁን በማጉደፍ አትርከሱ

ርኩስ እንስሳ እንዳይበሉ ያዘዛቸውን ትዕዛዝ ለማጠንከር እግዚአብሔር ሁለት ጊዜ ተመሣሣይ ሃሳብ ይደግማል:: (ተጓዳኝ ንጽጽር ይመልከቱ)

ራሳችሁን አታርክሱ

ለእግዚአብሔር ዓላማ ያልተገባ ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እንግዲህ በእነርሱ ራሳችሁን ታጐድፋላችሁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል አት እንግዲህ ከእነርሱ የተነሣ ንጹሃን አትሆኑም (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 11:46

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሕዝቡ ምን እንዲበላ እንደፈቀደና ምን እንዳይበላ እንደከለከለ ለሙሴና ለአሮን በመናገር ያበቃል

መለየት ስላለባቸው ነገሮች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል አት እናንተ መለየት ስለአለባችሁ ነገሮች (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በእርኩሱና በንጹሑ መካከል

ሕዝቡ እንዲነካና እንዲበላ የተገባቸው እግዚአብሔር የተናገራቸው እንስሳት በአካል ርኩስ ተብለዋል እና ሕዝቡ እንዲነካና እንዲበላ የተነገራቸው በአካል ንጹህ ተብለዋል ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ

የሚበላውና የማይበላው

ይህ በተሻጋሪ ግሥ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፡ የሚትበሉትንና የማትበሉትን፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)


Chapter 12

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “ለእስራኤል ሰዎች እንደህ በላቸው፣ ‘አንዲት ሴት ብታረግዝና ወንድ ልጅ ብትወልድ፣ ልክ እንደ ወር አበባዋ ወቅት ለሰባት ቀናት ንጹህ አይደለችም፡፡ 3 በስምንተኛው ቀን ህጻኑ ልጅ መገረዝ አለበት፡፡ 4 ከዚያ የእናቲቱ ከደሟ መንጻት ለሰላሳ ሶስት ቀናት ይቆያል፡፡ ምንም አይነት የተቀደሰ ነገር መንካት የለባትም ወይም የመንጻቷ ቀናት እስኪፈጸም ድረስ ወደ ቤተመቅደስ አትምጣ፡፡ 5 ሴት ልጅ ከወለደች፣ በወር አበባዋ ወቅት እንደነበረችው ለሁለት ሳምንታት ንጹህ አትሆንም፡፡ ከዚያ የእናትየው የመንጻት ስርዓት ለስድስት ቀናት ይቀጥላል፡፡ 6 ወንድ ልጅም ሆነ ሴት ልጅ ከወለደች በኋላ የመንጻቷ ቀናት ሲያበቃ ለካህኑ በመገናኛው ድንኳን መግቢያ የአንድ አመት ጠቦት ለሚቃጠል መስዋዕት እንዲሁም ለኃጢአት መስዋዕት ዋኖስ ወይም ዕርግብ ታቅርብ፡፡ 7 ከዚያ ካህኑ መስዋዕቱን በያህዌ ፊት ይሰዋና ያስተሰርይላታል፣ እናም ከደሟ መፍሰስ ንጹህ ትሆናለች፡፡ ወንድም ይሁን ሴት ልጅ ለወለደች ሴት ህጉ ይህ ነው፡፡ 8 ጠቦት ማቅረብ ባትችል፣ ሁለት ዋኖሶች ወይም ሁለት ርግቦች ትውሰድ፣ አንዱን ለሚቀጠል መስዋዕት ሌላውን ለኃጢአት መስዋዕት ታቅርብ እናም ካህኑ ያስተሰርይላታል፣ ከዚያም ንጹህ ትሆናለች፡፡’”



Leviticus 12:1

ትረክሳለች

ከማዕጸንዋ ደም ስለሚፈስስ ሰዎች የማይነኩአት ሴት በአካል ርኩስ ተብላለች ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ

በወር አበባዋ ጊዜ

ይህ በወር ከማዕጸንዋ ደም የሚፈስስበት ጊዜ ያመለክታል (See Euphemism/ንኣብነት ወይም ጸያፍ አባበሎችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የወንድ ልጅ አካለ ብልት ቆዳ ይገረዝ

ካህኑ ብቻ ይህንን ድርጊት ይፈጽም ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል አት ካህኑ ወንድ ህጻን ልጅን ይገርዘው፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 12:4

አንድ እናት ከደሟ እንስኪትነጻ ድረስ ሠላሣ ሶስት ቀን ድረስ ትቆይ

ይህች እናት ለሠላሣ ሶስት ቀናት ርኩስ ትሆናለች ማለት ነው፡፡

ሠላሣ ሶስት ቀናት

33 ቀናት (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ለሁለት ሳምንታት ርኩስ ትሆናለች

ከማዕጸንዋ ደም ስለሚፈስሳት ሌሎች ሰዎች የማይነኳት ሴት በአካል ርኩስ ትብላለች፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ለሁለት ሣምንታት

14 ቀናት

ወር አበባዋ ጊዜ

ከማዕጸንዋ ደም የሚፈስስበት ወራዊ ጊዜ ያመለክታል በዘሌዋዊያን 12:2 እንዴት አንደተረጐሙ ይመልከቱ (See: Euphemism/ንኣብነት ወይም ጸያፍ/አሳፋሪ አባበሎችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ስድሳ ስድስት ቀናት

66 ቀናት

Leviticus 12:6

የመስጻትዋ ጊዜ ስፈጸም

የአንድ እናት የመንጻት ቀኖችዋ ሲፈጸም

ለወንድ ልጅ ወይም ለሴት ልጅ

ወንድ ልጅ ወይም ሴት ልጅ ወልዳ ከሆነ የአንዱ እናት የመንጻት ቀኖችዋ የተለያየ እንደሆነ ያመለክታል፡፡

Leviticus 12:7

ሴትዬዋ ከደሟ ፊሳሽ ትነጻለች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ይህ በወሊድ ጊዜ ከሚፈስሳት ደም ያነጻታል”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ጠቦት ለማምጣት አቅምዋ ካልፈቀደ

የመስዋዕት እንስሳ የመግዛት አቅም ማነስ በሚገልጽ መንገድ ይተርጉሙ፡፡ አት፡ “ጠቦት ለመግዛት በቂ ገንዘብ ከሌላት”

እርስዋም ትነጻለች:

ሌሎች ሰዎች መንካት የማችሏት ሴት በአካል ንጹህ ተብላለች፡፡


Chapter 13

1 ያህዌ ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፣ 2 “ማንኛውም ሰው በሰውነቱ ቆዳ ላይ እባጭ ወይም ችፍታ ወይም ቋቁቻ ቢወጣና ቢቆስል በሰውነቱ ላይ የቆዳ በሽታ ይሆናል፣ በዚህ ጊዜ ወደ ሊቀካህኑ አሮን ይምጣ፣ አሊያም ካህናት ከሆኑት ልጆቹ ወደ አንዱ ይምጣ፡፡ 3 ከዚያ በሰውነቱ ቆዳ ላይ ያለውን በሽታ ካህኑ ይመረምረዋል፡፡ በበሽታው ዙሪያ ያለው ጸጉር ወደ ነጭነት ከተለወጠ፣ እና በሽታው በቆዳው ላይ ከሚታየው ይልቅ የከፋ ሆኖ ከተገኘ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ ካህኑ ከመረመረው በኋላ፣ ንጹህ አለመሆኑን ያሳውቅ፡፡ 4 በቆዳው ላይ የታየው ቋቁቻ ነጭ ከሆነ፣ እና ወደ ቆዳው ዘልቆ የገባ ካልሆነ፣ እንዲሁም በህመሙ አካባቢ የሚገኘው ጸጉር ወደ ነጭነት ካልተለወጠ፣ ካህኑ በሽታው ያለበትን ሰው ለሰባት ቀናት ያገልግለው፡፡ 5 በሰባተኛው ቀን፣ ካህኑ በእርሱ እይታ በሽታው አየከፋ በቆዳው ላይ እየሰፋ አለመሄዱን ለማየት ይመርምረው፡፡ በሽታው ለውጥ ካላሳየ፣ ካህኑ ለተጨማሪ ሰባት ቀናት ሰውየውን አግልሎ ያቆየው፡፡ 6 በሰባተኛው ቀን በሽታው እየተሻለው እንደሆነና በቆዳው ላይ እየሰፋ እንደላሆነ ለማየት ካህኑ ሰውየውን ደግሞ ይመረምረዋል፡፡ በሽታው ለውጥ ካለው፣ ካህኑ ሰውየው ንጹህ መሆነኑን ይገልጻል፡፡ ይህ ሽፍታ ነው፡፡ ሰውየው ልብሱን ይጠብ፣ እናም ከዚህ በኋላ ንጹህ ነው፡፡ 7 ነገር ግን ሰውየው ራሱን ለካህን ካሳየ በኋላ ሽፍታው በቆዳው ላይ ከተስፋፋ፣ እንደገና ራሱን ለካህን ያሳይ፡፡ 8 ሽፍታው ይበልጥ በሰውየው ቆዳ ላይ እየሰፋ መሆኑን ለማየት ካህኑ ይመረምረዋል፡፡ ከተስፋፋ፣ ከዚያ ካህኑ ሰውየው ንጹህ አይደለም ይላል፡፡ ይህ ተላላፊ የቆዳ በሽታ ነው፡፡ 9 ተላላፊ የቆዳ በሽታ በአንድ ሰው ላይ ሲገኝ፣ ይህ ሰው ወደ ካህን ይምጣ፡፡ 10 ካህኑ በሰውየው ቆዳ ላይ ነጭ ዕብጠት መኖሩን ለማየት ይመረምረዋል፣ ጸጉሩ ወደ ነጭነት መቀየሩን፣ ወይም በዕብጠቱ ላይ የስጋ መላጥ መኖሩን ይመልከት፡፡ 11 እንዲህ ያለ ነገር ካለ፣ ይህ ጽኑ የቆዳ ህመም ነው፣ እናም ካህኑ ሰውየው ንጹህ አለመሆኑን ይግለጽ፡፡ ሰውየውን አያገለውም፣ ምክንያቱም ቀድሞውኑም ንጹህ አይደለም፡፡ 12 በሽታው በቆዳው ላይ በሰፊው ጎልቶ ከታየና የሰውየውን ቆዳ ከአናቱ እስከ እግሩ ከሸፈና፣ ካህኑ ይህ እስከ ታየው ድረስ፣ በሽታው የሰውየውን አካል ሸፍኖት እንደሆነ ለማየት ይመርምረው፡፡ 13 እንዲህ ሆኖ ከተገኘ፣ በሽታው ያለበት ሰው ንጹህ አለመሆኑን ካህኑ ይግለጽ፡፡ ሁሉም ወደ ንጣት ተለውጦ ከሆነ ንጹህ ነው፡፡ 14 ነገር ግን የስጋ መላጥ ከታየበት፣ ሰውየው ንጹህ አይደለም፡፡ 15 ካህኑ የስጋውን መላጥ ማየትና ንጹህ አለመሆኑን ይግለጽ፣ ምክንያቱም የተላጠ ስጋ ንጹህ አይደለም፡፡ ይህ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ 16 ነገር ግን የተላጠው ስጋ መለልሶ ነጭ ቢሆን፣ ሰውየው ወደ ካህኑ ይሂድ፡፡ 17 ካህኑ ስጋው ወደ ነጭነት ተመልሶ እንደሆነ ይመረምረዋል፡፡ እንዲህ ከሆነ ካህኑ ሰውየው ንጹህ መሆኑን ይገልጻል፡፡ 18 አንድ ሰው በቆዳው ላይ እባጭ ወጥቶ ሲድን፣ 19 እና በዕባጩ ስፍራ እብጠት ወይም ቋቁቻ፣ ቀላ ያለ ንጣት፣ ሲኖር ይህን ካህኑ ሊያየው ይገባል፡፡ 20 ካህኑ ይህ ወደ ታማሚው ቆዳ ዘልቆ የገባ መሆኑን እና በዚያ ዙሪያ ያለው ጸጉር ወደ ነጭነት መለወጡን ለማየት ይመረምራል፡፡ እንዲያ ከሆነ፣ ካህኑ ታማሚው ንጹህ አለመሆኑን ያሳውቃል፡፡ እብጠቱ በነበረበት ስፍራ እየሰፋ ከሄደ ይህ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ 21 ነገር ግን ካህኑ ይህንን መርምሮ በውስጡ ነጭ ጸጉር አለመኖሩን ከተመለከተ፣ እና ይህም ከቆዳው ስር ካልሆነ ሆኖም ከደበዘዘ ካህኑ ታማሚውን ለሰባት ቀናት ያግልለው፡፡ 22 በቆዳው ላይ በሰፊው ከተስፋፋ፣ ካህኑ ታማሚው ንጹህ አይደለም ይበል፡፡ ይህ የሚተላለፍ በሽታ ነው፡፡ 23 ነገር ግን ቋቁቻው በቦታው ከሆነና ካልተስፋፋ፣ ይህ የእባጩ ጠባሳ ነው፣ እናም ካህኑ ንጹህ ነው ብሎ ያስታውቅ፡፡ 24 አንድ ሰው ቆዳው ቃጠሎ ሲኖርበትና የስጋው መላጥ ቀላ ያለ ንጣት ወይም ነጭ ጠባሳ ሲሆን፣ 25 ካህኑ ያጠባሳ ስፍራ ወደ ንጣት መለወጡን እና ወደ ቆዳው ዘልቆ መግባቱን ለማየት ይመረምራል፡፡ እንደዚህ ከሆነ፣ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ ከቃጠሎው አልፎ ከውስጥ የመጣ ነው፣ እናም ካህኑ ሰውየው ንጹህ አለመሆኑን ያሳውቅ፡፡ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ 26 ነገር ግን ካህኑ በሚመረምርበት ጊዜ በስፍራው ነጭ ጸጉር አለመኖሩን ቢደርስበትና ቁስሉ ከቆዳው ስር ሳይሆን ቢቀር እየከሰመ ቢመጣ ካህኑ ታማሚውን ለሰባት ቀናት ያግልለው፡፡ 27 ከዚያም ካህኑ በሰባተኛው ቀን ይመርምረው፡፡ ምልክቱ በሰፊው በቆዳው ላይ ቢስፋፋ፣ ካህኑ ንጹህ አይደለም ብሎ ያሳውቅ፡፡ ይህ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ 28 ምልክቱ በስፍራው ከቆየና በቆዳው ላይ እየሰፋ ካልሄደ ነገር ግን ከከሰመ ይህ በቃጠሎው የመጣ እብጠት ነው፣ እናም ካህኑ ሰውየው ንጹህ መሆኑን ያሳውቅ፣ ይህ ከቃጠሎው የመጣ ጠባሳ እንጂ ሌላ ነገር አይደለም፡፡ 29 በአንድ ወንድ ወይም ሴት ራስ ወይም አገጭ ላይ ተላላፊ በሽታ ቢኖር፣ 30 ችግሩ ከቆዳው ስር የዘለቀ መሆኑና በላዩ ቢጫ ስስ ጸጉር እንዳለ ለማየት ካህኑ ካህኑ የተላላፊ በሽታ ምርመራ ያድርግለት፡፡ ይህ ከተገኘ፣ ካህኑ ሰውየው ንጹህ አለመሆኑን ያሳውቅ፡፡ ይህ የሚያሳክክ በሽታ ነው፣ በራስ ወይም አገጭ ላይ የወጣ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ 31 የሚያሳክከውን በሽታ መርምሮ ከቆዳ ስር ያልዘለቀ መሆኑን ቢያይ፣ ደግሞም በውስጡ ጥቁር ጸጉር ባይኖር፣ ካህኑ ሰውየውን በሚያሳክክ በሽታው ምክንያት ለሰባት ቀናት ያግልለው፡፡ 32 በሰባተኛው ቀን በሽታው ተስፋፍቶ እንደሆነ ለማየት ካህኑ ይመረምረዋል፡፡ ቢጫ ጸጉር ከሌለና፣ በሽታው ላይ ላዩን ብቻ ከታየ፣ 33 ሰውየው ይላጭ፣ ነገር ግን በሽታው የሚገኝበት ዙሪያ መላጨት የለበትም፣ እናም ካህኑ የሚያሳክክ በሽታ ያለበትን ሰው ለሰባት ቀናት ያግልለው፡፡ 34 በሰባተኛው ቀን በሽታው በቆዳው ላይ መስፋፋቱን ማቆሙን ለማየት ካህኑ ምርመራ ያደርጋል፡፡ በሽታው ቆዳውን ዘልቆ የገባ ካልሆነ፣ ካህኑ የሰውየውን ንጹህ መሆን ያሳውቅ፡፡ ሰውየው ልብሱን ይጠብ፣ እናም ከዚያ ንጹህ ይሆናል፡፡ 35 ነገር ግን ካህኑ ንጹህ መሆኑን ካሳወቀ በኋላ የሚያሳክከው በሽታ እየሰፋ ከሄደ ፣ 36 ካህኑ ዳግም ይመርምረው፡፡ በሽታው በሰውየው ቆዳ ላይ እየሰፋ ከሄደ፣ካህኑ ቢጫ ጸጉር መኖሩን መፈለግ አይኖርበትም፡፡ ሰውየው ንጹህ አይደለም፡፡ 37 ነገር ግን ካህኑ ሰውየውን የሚያሳክከው በሽታ እየሰፋ መሄዱን እንዳቆመ ከተመለከተ ንጹህ መሆኑን ያሳውቅ፡፡ 38 አንድ ወንድ ወይም አንዲት ሴት በቆዳቸው ላይ ነጭ ምልክቶች ቢወጣ 39 ምልክቱ ዳለቻ መልክ ያለው በቆዳ ላይ የወጣ ሽፍታ ብቻ መሆኑን ለማየት ካህኑ ምርመራ ያድርግ፡፡ ሰውየው ንጹህ ነው፡፡ 40 የሰውየው ጸጉር ከራሱ ላይ ካለቀ፣መላጣ ነው፣ ነገር ግን ንጹህ ነው፡፡ 41 ደግሞም ከፊት ለፊት ጸጉሩ ተመልጦ ራሰ በራ ቢሆንም ንጹህ ነው፡፡ 42 ነገር ግን በህመም ምክንያት ፈዘዝ ያለ ቅላት በተመለጠው ራሱ ላይ ወይም በግምባሩ ላይ ቢኖር፣ ይህ በተላላፊ በሽታ ምክንያት የመጣ ነው፡፡ 43 በቆዳ ላይ ተላላፊ በሽታ ሲኖር እንደሚታየው በመላጣው ወይም በበራው ላይ በህመሙ ዙሪያ ፈዘዝ ያለ ቅላት መኖሩን ለማየት ካህኑ ምርመራ ያድርግለት፡፡ 44 ይህ ከሆነ፣ ተላላፊ በሽታ አለበት እናም ንጹህ አይደለም፡፡ በእርግጥ ካህኑ ሰውየው በራሱ ላይ ካለበት በሽታ የተነሳ ንጹህ እንደልሆነ ያስታውቅ፡፡ 45 ተላላፊ በሽታ ያለበት ሰው የተቀደደ ልብስ ይልበስ፣ ጸጉሩን በከፊል ይሸፍን፣ እስከ አፍንጫው ይከናነብና ‘እርኩስ ነኝ፣ እርኩስ ነኝ’ እያለ ይጩህ፡፡ 46 ተላላፊው በሽታ ባለበት ቀናት ሁሉ እርኩስ ነው፡፡ እየሰፋ ሊሄድ በሚችል በሽታ ምክንያት ንጹህ ስላልሆነ፣ ለብቻው ይኑር፡፡ ከሰፈር ውጭ ይኑር፡፡ 47 በማናቸውም ነገር የተበከለ የሱፍም ሆነ የተልባ ዕግር ጨርቅ፣ 48 ወይም ከሱፍም ሆነ ከተልባ ዕግር ጨርቅ የተፈተለ፣ ወይም ቆዳም ሆነ ከቆዳ በተሰራ ልብስ - 49 በልብሱ ላይ አረንጓዴ ወይም ቀላ ያለ ብክለት ቢገኝበት፤ በቆዳው፣ በተጠለፈው ወይም በተሰፋው ነገር፣ ወይም ማናቸውም ከቆዳ በተሰራው ነገር ለይ ብክለቱ እየሰፋ ቢሄድ ካህኑ ይህን ይመልከት፡፡ 50 ካህኑ የሚበከለውን ዕቃ ይመርምር፣ የተበከለውን ማናቸውንም ነገር ለሰባት ቀናት ይለየው፡፡ 51 በሰባተኛው ቀን እንደገና ብክለቱን ይመርምር፡፡ በልብሱ ወይም ከሱፍ ወይም ከተልባ ዕግር ጨርቅ በተሸመነው ወይም በተጠለፈው ማናቸውም ልብስ ላይ ብክለቱ እየሰፋ ቢሄድ ወይም በቆዳ ወይም ከቆዳ በተሰራ ማናቸውም ነገር ላይ ብክለቱ ቢሰፋ ጎጁ ነው፣ እናም ዕቃው ንጹህ አይደለም፡፡ 52 ካህኑ ያንን ልብስ ያቃጥል፣ ወይም ማናቸውም ከሱፍ ወይም ከተልባ ዕግር ጨርቅ የተፈተለ ወይም ቆዳ ወይም ከቆዳ የተሰራ ነገር፣ ማናቸውም ጎጂ ብክለት የተገኘበት ነገር በሽታ ያመጣልና ያቃጥለው፡፡ ዕቃው ሙሉ ለሙሉ ይቃጠል፡፡ 53 ካህኑ ዕቃውን መርምሮ ብክለቱ በልብ ወይም በተሸመነው ወይም በተለጠፈው ልብስ ወይም በቆዳ ዕቃዎቹ ላይ እየሰፋ የሚሄድ አለመሆኑን ካወቀ፣ 54 ብክለቱ የተገኘባቸውን ዕቃዎች እንዲያጥቡ ያዛቸዋል፤ ደግሞም ዕቃውን ለሰባት ቀናት ያግልል፡፡ 55 ከዚያ ካህኑ የተበከለውን ዕቃ ከታጠበ ከሰባት ቀናት በኋላ ይመረምረዋል፡፡ ብክለቱ ቀለሙን ካልቀየረውና እየሰፋ ባይሄድ እንኳን ንጹህ አይደለም፡፡ ብክለቱ የትም ላይ ይሁን ዕቃዎቹን አቃጥሏቸው፡፡ 56 ካህኑ ዕቃውን ከመረመረና ልብሱ ከታጠበ በኋላ ብክለቱ እየለቀቀ ከሄደ፣ ከተበከለው የልብሱ ወይም የቆዳው ክፍል ወይም ከተሸመነው ወይም ከተጠለፈው ዕቃ ቀድዶ ያውጣው፡፡ 57 እንዲህም ሆኖ ብክለቱ አሁንም በተሸመነው ወይም በተጠለፈው፣ ወይም በማናቸውም ከቆዳ በተሰራው ነገር ላይ ከተገኘ እየሰፋ በመሄድ ላይ ነው፡፡ ብክለት ያለበትን ማናቸውንም ነገር አቃጥለው፡፡ 58 ከሱፍ ወይም ከተልባ ዕግር ጨርቅ የተሰራ ወይም የተለጠፈ ልብስ ወይም ማናቸውም ነገር፣ ወይም ቆዳ ወይም ከቆዳ የተሰራ ማናቸውም ነገር - ስታጥበው ብክለቱ እየለቀቀ ከሄደ፣ ዕቃው ዳግመኛ ይታጠብ እናም ንጹህ ይሆናል፡፡ 59 ከሱፍ ወይም ከተልባ ዕግር ጨርቅ ለተሸመነ ወይም ለተጠለፈ፣ከሱፍ ወይም ከተልባ ዕግር ጨርቅ ወይም ቆዳ ወይም ከቆዳ ለተሰራ ማናቸውም ነገር ብክለት ህጉ ይህ ነው፣ ስለዚህ ንጹህ ነው ወይም እርኩስ ነው ብለህ ማሳወቅ ትችላለህ፡፡”



Leviticus 13:1

ከዚያም ያምጡት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ከዚያም አንድ ሰው ያምጣው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ከልጆቹ ወደ አንዱ

ከአሮን ልጆች ወደ አንዱ

Leviticus 13:3

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን መናገር ቀጠለ

የእርሱ ሰውነት ቆዳ ወይም የሰውነቱ ቆዳ

እዚህ እርሱ የቆዳ በሽታ ያለበትን ሰው ያመለክታል

ተላላፊ በሽታ

ከአንድ ሰው በቀላሉ ወደ ሌላው መተላለፍ የሚችል በሽታ

እርሱም ሰውየው ርኩስ መሆኑን ይግለጽ

ካህኑም ሰውየው ርኩስ መሆኑን ይግለጽ፡፡ ሌሎች ሰዎች የማይነኩት ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ለሰባት ቀናት

“ለ 7 ቀናት ቁጥሮችን ይመልከቱ”

Leviticus 13:5

እርሱን ካህኑ ይመረምረው

እዚህ እርሱ የቆዳ በሽታ ያለበትን ሰው ያመለክታል

በቆዳውም ላይ ካልተስፋፋ

ይህም የቆዳው በሽታ መጠኑን ካልጨመረ ወይም ወደ ሌላው የሰውነት አካል ካልተላለፈ ማለት ነው

ሰባተኛው ቀን

“ቀን 7” (ተራ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ሰባት ቀናት

“7 ቀናት” (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ካህኑ ንጹህ ስለመሆኑ ይግለጽ…ንጹህም የሆናል

ሌሎች ሰዎች መንካት የሚችሉት ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ

ችፍታ

ይህ የሚያስከፋ የቆዳ አካል ነው ፤ነገር ግን ወደ ሌላ ሰው የማይተላለፍ ነው፡፡

Leviticus 13:7

ራሱ…ብቻውን

በሽታው ያለበትን ሰው ያመለክታል

ካህኑ ርኩስ ስለመሆኑ ይግለጽ

ሌሎች ሰዎች የማይነኩት ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ተላላፊ በሽታዎች

በዘሌዋዊያን 13፡3 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

Leviticus 13:9

ወደ ካህኑ ያምጡት

በሽታው ተሠራጭቶ እንደሆነ ካህናት ይወስናሉ:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “አንድ ሰው ወደ ካህኑ ያምጣው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እብጠቱ ውስጥ ቀይ ሥጋ ቢታይ

እዚህ ቀይ ሥጋ በእባጩ ላይ የተከፈቱ ቁስሎችን ወይም አዲስ ቆዳ ያደገውን ነገር ግን ዙሪያው እንደቆሰለ እንዳለ የሚያመለክት ነው፡፡

ሥር የሰደደ የቆዳ በሽታ

ይህ የተደገመ ወይም ለረጅ ጊዜ በተደጋጋሚ የሚከሰት ነው፡፡

ሰውየው ርኩስ መሆኑን ካህኑ ያስታውቅ … ርኩስ መሆኑም ግልጽ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች ሊነኩት የማይችሉት ሰው በአካል ርኩስ ይባላል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 13:12

አጠቃላይ መረጃ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል

ካህኑ ሰውየውን ያስታውቅ … ንጹህ …. ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች ሊነኩት የሚችሉት ሰው በአካል ንጹህ ይባላል፤ እናም ሌሎች ሰዎች ሊነኩት የማይችሉት ሰው በአካል ርኩስ ይባላል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 13:15

ካህኑ…ርኩስ መሆኑን ያሰታውቅ ምክንያቱም ቀይ ሥጋ ርኩስ ስለሆነ

ሌሎች ሰዎች የማይነኩት ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እርሱ ርኩስ መሆኑን ያሰታውቅ

እዚህ ርኩስ የቆዳ በሽታ ያለበትን ሰው ያመለክታል

ቀይ ሥጋ

በዘሌዋዊያን 13፡1ዐ ይህን እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ተላላፊ በሽታዎች

በዘሌዋዊያን 13፡3 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ሰውየው ንጹህ መሆኑን ካህኑ ያስታውቃል

ሌሎች ሰዎች የሚነኩት ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:18

አጠቃላይ መረጃ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል

ዕባጭ

የሚያምም እብጠት የያዘ የቆዳ አካል ነው

ካህኑ ዘንድ ቀርቦ መታየት አለበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱም ካህኑን ያሳየው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ርኩስ መሆኑን ካህኑ ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:21

አጠቃላይ መረጃ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል

ይህን ይመረምረው

እዚህ “ይህ” በቆዳው ላይ የሚታይ ነጭ እብጠት ቀላ ያለ ነገር ማለት ነው

ርኩስ መሆኑን ካህኑ ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ካህኑም ንጹህ መሆኑን ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች የማነካው ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:24

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ተላላፊ በሽታዎች

በዘሌዋዊያን 13፡3 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ርኩስ መሆኑን ካህኑ ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:26

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ይህን ይመረምረው

እዚህ “ይህ” በቆዳው ላይ የሚታይ ነጭ ጠባሳ ነገር ማለት ነው

ሰውየው ርኩስ መሆኑን ካህኑ ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ተላላፊ በሽታዎች

በዘሌዋዊያን 13፡3 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ካህኑ ንጹህ መሆኑን ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች የሚነካው ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:29

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ያ ሰው ርኩስ መሆኑን ካህኑ ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች መንካት የማይገባው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:31

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

Leviticus 13:32

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ጸጉሩን ይላጭ ነገር ግን በቆሰለው ቦታ ያለውን አይላጭ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ሰውየው በቁስሉ ላይ ያለውን ጸጉር ሳይሆን በቁስሉ ዙሪያ ያለውን ጸጉር ይላጭ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:34

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

የሚያሳክክ ቁስል

እዚህ የሚያሳክክ ቁስል በሰውየው ራስ ወይም ጉንጭ ላይ የሚታይ የሚያሳክክ ቁስል ያመለክታል ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ

ካህኑ ንጹህ መሆኑን ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች የሚነካው ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:35

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ንጹህ መሆኑን ካህኑ ከተናገረ … ሰውየው ነጽቶአል ካህኑም ንጹህ መሆኑን ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች መንካት የሚገባው ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሰውየው ርኩስ ነው

ሌሎች ሰዎች መንካት የማይገባው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:38

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ቋቁቻ

ደለቻ/ደብዛዛ ነጭ ነገር

ሽፍታ

በዘሌዋዊያን 13:6 ይህን ቃል እንዴት አንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ሰውየውም/እርሱ ንጹህ ነው

እዚህ “እርሱ” በአጠቃላይ ለወንዶችና ለሴቶች እንዴሚውል ያመለክታል: አት: “ያ ሰው ንጹህ ነው” (የወንድ ጾታ ቃላት ሴት ጾታን ስለማካተት ይመልከቱ)

ሰውየው ንጹህ ነው

ሌሎች ሰዎች መንካት የሚገባው ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:40

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ሰውየው ንጹህ ነው

ሌሎች ሰዎች መንካት የሚገባው ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:42

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ተላላፊ በሽታ

በዘሌዋዊያን 13:3 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

እርሱ ርኩስ ነው…ርኩስ መሆኑን ያስታውቅ

ሌሎች ሰዎች መንካት የማይገባው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:45

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው የቆዳ በሽታ ሲኖረው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ከሠፈር ውጪ

ሠፈር አብዛኛው እስራኤላዊያን የሚኖሩበት ቦታ ነው በሽታው ወደሌላ ሰው ስለሚዛመት ወይም ስለሚተላለፍ ንጹህ ያለሆነው ሰው በመካከላቸው እንደኖር አልተፈቀደም

ርኩስ ርኩስ

ሌሎች ሰዎች መንካት የማይገባው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:47

አረንጓዴ ወይም ቀይ መሣይ ደዌ የተበከለ ልብስ

አረንጓደ ወይም ቀይ መሣይ ደዌ በላይ ላዩ ያለው ልብስ ወይም በለምጽ ደዌ የተበከለ ልብስ

ተበከለ

በላዩ ላይ ጐጂ ነገር ስለታየበት ርኩስ ነው

ቀይ ወይም አረንጓዴ ደዌ

በርጥብና በተጣሉ ነገሮች ላይ የሚበቅል በአብዛኛው ነጭ ሻገታ ፋንገስ ነው

በሸማኔ ዕቃ በተሠራ ወይም በእጅ በተጠለፈ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “አንድ ሰው በሸማኔ ዕቃ ወይም በእጅ የሠራውን ማንኛው ነገር”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በልብስ ላይ አረንጓዴ ወይም ቀይ መሣይ የተበከለ ነገረ ቢገኝ

“አረንጓዴ ወይም ቀይ መሣይ ዴዌ በልብስ ላይ ቢገኝ”

ከቆዳ የተሠራ ዕቃ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “አንድ ሰው ከቆዳ የሠራው ማንኛው ነገር”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ይህ ለካህኑ ይታይ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “የዕቃው ባለቤት ለካህኑ ያሣየው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 13:50

ሰባት ቀናት

“7 ቀናት” (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ሰባተኛ ቀን

“ሰባተኛ ለተራ ቁጥር 7 ነው”፡፡ (ተራ ቁጥሮች ይመልከቱ)

ማንኛውንም ቆዳ የተጠቀመበት ዕቃ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “አንድ ሰው ቆዳን የተጠቀመበቅ ማንኛውም ነገር”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ጐጂ ደወው ያለበት ማንኛውም ነገር ቢገኝ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ማንኛውንም ጐጂ ደወው ያለበትን ነገር ቢያገኝ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ዕቃው ርኩስ ነው

ሕዝቡ እንዲነካ ያልተገባው ማንኛውም ነገር በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ይህ በሽታን ሊያስይዝ ይችላል

ክፉ ደወው ዕቃውን የሚነካውን ሰው በሽታ ሊያስይዝ ይችላል

ዕቃው ሙሉ በሙሉ ይቃጠል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ዕቃውን ፈጽሞ ያቃጥለው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

Leviticus 13:53

ይዘዝ

የዕቃው ባለቤቶችን ካህኑ ይዘዝ እዚህ ሕዝቡ የተበከሉ የቤት ዕቃዎችን ምን ማድረግ እንዳለባቸው ካህኑ ይናገራቸዋል

ክፉ ደዌ የተገኘበት ነገር

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ክፉ ደዌውን ያገኙበት ነገር”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ደዌው ያለበት ነገር ከታጠበ በኋላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ዴዌው ያለበትን ነገር ካጠቡ በኋላ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ርኩስ ነው

ሕዝቡ እንዲነካ ያልተገባው ማንኛውም ነገር በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እርሱ ዕቃው በእሳት ይቃጥል

እዚህ እርሱ ካህኑን አያመለክትም አንድ ሰው ዕቃውን ያቃጥል ማለት ነው፡፡

Leviticus 13:56

ዕቃው ከታጠበ በኋላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ባለቤቱ ካጠበው በኋላ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

እርሱም በእሳት ያቃጥል

እዚህ እርሱ በተለይ ካህኑን የሚያመለክት አይደለም አንድ ሰው ዕቃውን ማቃጠል አለበት ማለት ነው

ዕቃውን የሚያጥብ ከሆነ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ባለቤቱ የሚያጥብ በኋላ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ንጹሕም ይሆናል

ሕዝቡ እንዲነካ የተገባው ማንኛውም ነገር በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 13:59

ከቆዳ የተሠራው ማንኛውም ዕቃ በደዌ ቢበከል

በዘሌዋዊያን 13፡47-48 እንነዚህን ቃላት እንዴት አንደተረጐሙ ይመልከቱ፡፡

ስለሆነም ይህን ያስታውቀው

ስለሆነም ካህኑ ያስታውቀው

ንጹህ ወይም ርኩስ

ሕዝቡ እንዲነካ የተገባው ማንኛውም ነገር በአካል ንጹህ ተብሎአል:: እናም ሕዝቡ እንዲነካ ያልተገባው ማንኛውም ነገር በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)


Chapter 14

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “የታመመ ሰው በሚነጻበት ቀን ህጉ ይህ ነው፡፡ ወደ ካህኑ ይቅረብ፡፡ 3 ካህኑ የሰውየው ተላላፊ የቆዳ በሽታ መዳኑን ለመመርመር ከሰፈር ይወጣል፡፡ 4 ከዚያም ካህኑ የሚነጻው ሰው ህይወት ያላቸው ሁለት ንጹህ ወፎችን፣ የጥድ ዕንጨት፣ ደማቅ ቀይ ድርና ሂሶጵ እንዲያመጣ ያዘዋል፡፡ 5 ካህኑ የታመመው ሰው ከወፎቹ አንዱን አርዶ በሸክላ ማሰሮ ውስጥ እንዲጨምር ያደርጋል፡፡ 6 ከዚያ ካህኑ ህይወት ያለውን ወፍ፣የጥዱን እንጨትና፣ ደማቁን ቀይ ድርና ሂሶጵ ይቀበለውና ህይወት ያለውን ወፍ ጨምሮ እነዚህን ነገሮች በሙሉ ቀደም ሲል በታረደው ወፍ ደምና ንጹህ ውሃ ውስጥ ይከታቸዋል፡፡ 7 ከዚያ ካህኑ ይህንን ውሃ ከበሽታው በሚነጻው ሰው ላይ ሰባት ጊዜ ይረጫል፣ ከዚያ በኋላ ካህኑ ሰውየው ንጹህ መሆኑን ያሳውቃል፡፡ ከዚያ ካህኑ ህይወት ያለውን ወፍ ወደ ሜዳ ይለቀዋል፡፡ 8 የነጻው ሰው ልብሱን ያጥባል፣ ፀጉሩን በሙሉ ይላጫል፣ገላውንም ይታጠባል፤ ከዚህ በኋላ ንጹህ ይሆናል፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ ሰፈር ይመለስ፣ ነገር ግን ከድንኳኑ ውጭ ለሰባት ቀናት ይቆያል፡፡ 9 በሰባተኛው ቀን የራሱን ፀጉር በሙሉ ይላጭ፣ ልብሶቹን ይጠብ፣ ገላውን በውሃ ይታጠብ፤ ከዚህ በኋላ ንጹህ ይሆናል፡፡ 10 በስምንተኛው ቀን ነውር የሌለባቸው ሁለት ወንድ የበግ ጠቦቶች፣አንድ ነውር የሌለበት የአንድ አመት የበግ ጠቦት ያምጣ፣ በዘይት የተለወሰ የኢፍ ሶስት አስረኛ የላመ ዱቄት እና አንድ ሊትር ዘይት ለእህል ቁርባን ያቅርብ፡፡ 11 የመንጻት ስርዓቱን የሚያስፈጽመው ካህን የሚነጻውን ሰው ከእነዚህ ነገሮች ጋር ይዞ፣ በያህዌ ፊት በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ ይቆማል፡፡ 12 ካህኑ ወንዱን ጠቦት ወስዶ ለኃጢአት መስዋዕት ከአንዱ ሊትር ዘይት ጋር ያቀርባል፤ እነዚህንም በያህዌ ፊት ለመስዋዕት ይወዘውዘዋል፤ ለእርሱም ያቀርበዋል፡፡ 13 ወንዱን ጠቦት የኃጢአት መስዋዕቱንና የሚቃጠል መስዋዕቱን ባቀረቡበት ስፍራ በቤተ መቅደስ ያርደዋል፤ እንደ በደል መስዋዕቱ ሁሉ የኃጢአት መስዋዕቱም ለካህኑ ይሰጥ፣ ምክንያቱም ይህ እጅግ ቅዱስ ነው፡፡ 14 ካህኑ ከበደል መስዋዕቱ ጥቂት ደም ወስዶ በሚነጻው ሰው ቀኝ ጆሮ ጫፍ፣ በቀኝ እጁ አውራ ጣት ላይ እና በቀኝ እግሩ አውራ ጣት ላይ ይቀባ፡፡ 15 ከዚያ ካህኑ ከዘይቱ ወስዶ በእርሱ በራሱ ግራ እጅ መዳፍ ላይ ያፈሳል፣ 16 ከዚያም በግራ እጁ መዳፍ ላይ በፈሰሰው ዘይት ውስጥ የቀኝ እጁን ጣት ያጠልቃል፣ በጣቱ ላይ ካለው ዘይት በያህዌ ፊት ሰባት ጊዜ ይረጫል፡፡ 17 ካህኑ በእጁ ላይ የቀረውን ዘይት በሚነጻው ሰው ቀኝ ጆሮ ጫፍ፣ በቀኝ እጁ አውራ ጣት፣ እና በቀኝ እግሩ አውራ ጣት ላይ ይቀባል፡፡ ይህንን ዘይት በበደል መስዋዕቱ ደም ላይ ያድርገው፡፡ 18 ካህኑ በእጁ የቀረውን ዘይት፣ በሚነጻው ሰው ራስ ላይ ያፍስስ፣ እናም ካህኑ በያህዌ ፊት የሚነጻውን ሰው ያሰርይለታል፡፡ 19 ከዚያ ካህኑ የኃጢአት መስዋዕቱን ይሰዋል፤ ደግሞም ንጹህ ባለመሆኑ ምክንያት መንጻት ላለበት ሰው ያሰርይለታል፣ እናም ከዚህ በኋላ የሚቃጠል መስዋዕቱን ይሰዋል፡፡ 20 ካህኑ የሚቃጠለውን መስዋዕትና የእህል ቁርባኑን በመሰዊያ ላይ ያቀርባል፡፡ ካሁኑ ለሰውየው ማስተስረያ ያቀርብለታል፡፡ ከዚያ ንጹህ ይሆናል፡፡ 21 ሆኖም ሰውየው ደሃ ከሆነና እነዚህን መስዋዕቶች ማቅረብ ካልቻለ ለኃጢአቱ ማስተስረያ የበደል መስዋዕት አንድ ወንድ ጠቦት፣ በዘይት የተለወሰ የኢፍ አንድ አስረኛ መልካም ዱቄትና አንድ ሊትር ዘይት ያቅርብ፣ 22 ሰውየው በአቅሙ ከሁለት ርግቦች ወይም ሁለት ዋኖሶች ጋር፣ አንደኛውን ወፍ የኃጢአት መስዋዕት ሌላኛው ደግሞ የሚቃጠል መስዋዕት ያቀርባል፡፡ 23 በስምንተኛው ቀን ስለ መንጻቱ ወደ መገናኛው ድንኳን በያህዌ ፊት ያምጣቸው፡፡ 24 ከዚያ ካህኑ ጠቦቱን ለበደል መስዋዕት ደግሞም አንዱን ሊትር ዘይት፣ይወስድና ለያህዌ የበደል መስዋዕት ይወዘውዛል፣ እናም ለእርሱ እነዚህን ያቀርባቸዋል፡፡ 25 ለበደል መስዋዕት ጠቦቱን ያርዳል፣ እናም ከበደል መስዋዕቱ ጥቂት ደም ይወስድና በሚነጻው ሰው ቀኝ ጆሮ ጫፍ፣ በቀኝ እጁ አውራ ጣት ላይና በቀኝ እግሩ አውራ ጣት ላይ ይቀባል፡፡ 26 ከዚያ ካህኑ ከዘይቱ ጥቂቱን በገዛ ራሱ ግራ እጅ መዳፍ ላይ ያፈሳል፣ 27 በቀኝ ጣቱ ከዘይቱ በግራ እጁ በያህዌ ፊት ሰባት ጊዜ ይረጫል፡፡ 28 ከዚያ ካህኑ በእጁ ካለው ዘይት ጥቂቱን በሚነጻው ሰው ቀኝ ጆሮ ጫፍ ላይ፣ በቀኝ እጁ አውራ ጣት ላይና በቀኝ እግሩ አውራ ጣት ላይ የበደል መስዋዕቱን ደም ባደረገበት ተመሳሳይ ስፍራዎች ይቀባል፡፡ 29 የተረፈውን በእጁ ያለውን ዘይት ያስተሰርይለት ዘንድ በያህዌ ፊት በሚነጻው ሰው ራስ ላይ ያፈሳል፡፡ 30 ሰውየው በአቅሙ ካቀረበው ከእርግቦቹ ወይም ከዋኖሶቹ አንዱን ይሰዋ - 31 ከእህል ቁርባኑ ጋር፣ አንዱን ለኃጢአት መስዋዕት ሌላውን ለሚቃጠል መስዋዕት ያቅርብ፡፡ ከዚያም ካህኑ ለሚነጻው ሰው በያህዌ ፊት ያስተሰርይለታል፡፡ 32 ለመንጻት ዋናውን መስዋዕት ማቅረብ ለማይችል ተላላፊ የቆዳ በሽታ ላለበት ሰው የመንጻት ህጉ ይህ ነው፡፡” 33 ያህዌ ሙሴንና አሮንን እንዲህ ሲል ተናገራቸው፣ 34 “ርስት አድርጌ ወደሰጠኋችሁ ወደ ከነዓን ምድር ስትመጡ፣ ርስት በሆናችሁ ምድር በቤታችሁ እየሰፋ የሚሄድ ብክለት ባደርግባችሁ፣ 35 የቤቱ ባለቤት ወደ ካህኑ መጥቶ ይናገር፡፡ እንዲህም ይበል፣ “በቤቴ ብክለት ያለ ይመስለኛል፡፡’ 36 ከዚያ ካህኑ በቤቱ ውስጥ የሚገኝ ማናቸውም ነገር እርኩስ እንዳይሆን ብክለት መኖሩን ለማየት ወደዚያ ቤት ከመግባቱ አስቀድሞ ቤቱን ባዶ እንዲያደርጉ ያዛል፣ ከዚህ አስቀድሞ ካህኑ ያንን ቤት ለማየት ይገባል፡፡ 37 ሻጋታው በቤቱ ግድግዳዎች ላይ መኖሩን፣ ደግሞም አረንጓዴ ሆኖ ወይም ቀላ ብሎ በግርግዳዎቹ ላይ መታየቱን ይመርምር፡፡ 38 ቤቱ ሻጋታ ካለው፣ ካህኑ ከዚያ ቤት ይወጣና ለሰባት ቀናት በሩን ይዘጋዋል፡፡ 39 በሰባተኛው ቀን ካህኑ ተመልሶ ይመጣና ሻጋታው በቤቱ ግድግዳዎች ላይ መስፋፋቱን ለማየት ይመረምራል፡፡ 40 እንዲያ ከሆነ፣ ካህኑ ሻጋታ የተገኘባቸውን ድንጋዮች ከግድግዳው ላይ እየፈነቀሉ እንዲያወጡና ከከተማ ውጭ ቆሻሻ ስፍራ መጣያ እንዲጥሏቸው ያዛል፡፡ 41 የቤቱ የውስጥ ግድግዳዎች ሁሉ እንደዲፋቁ ይጠይቃል፣ እነርሱም እየተፋቁ የተነሱትን የተበከሉትን ቁሶች ከከተማ አውጥተው በቆሻሻ መጣያ ስፍራ ይጥላሉ፡፡ 42 ባስወገዷቸው ድንጋዮች ስፍራ ሌሎች ድንጋዮች ወስደው ያስቀምጡ፣ ቤቱን ለመምረግ አዲስ ጭቃ ይጠቀሙ፡፡ 43 ድንጋዮቹ ተነስተውና ግርግዳው ተፍቆ እንዲሁም ተለስኖ ዳግም ብክለቱ ከወጣና ከታየ፣ 44 ካህኑ ብክለቱ መስፋፋቱን ለመመልከት ቤቱን ይመርምር፡፡ እንዲያ ከሆነ፣ ይህ ጎጂ ብክለት ነው፤ ቤቱ ንጹህ አይደለም፡፡ 45 ቤቱ ይፍረስ፡፡ የቤቱ ድንጋዮች፣ በሮች፣ እና ፍርስራሾች ከከተማ ውስጥ በቆሻሻ መጣያ ይጣል፡፡ 46 በተጨማሪም፣ ቤቱ በተዘጋባቸው ጊዜያት ወደዚያ ቤት የሄደ ሁሉ እስከ ምሽት ድረስ እርኩስ ነው፡፡ 47 ማንም በዚያ ቤት ውስጥ የተኛ ሰው ልብሱን ይጠብ፣ እንዲሁም በዚህ ቤት ውስጥ የተመገበ ሰው ልብሱን ይጠብ፡፡ 48 ቤቱ ከተለሰነ በኋላ ብክለቱ ወዴት እንደተስፋፋ ለመመርመር ካህኑ ወደዚያ ቤት ቢገባ፣ እናም ብክለቱ ተወግዶ ቢሆን ቤቱ ንጹህ መሆኑን ያሳውቃል፡፡ 49 ከዚያ ካህኑ ቤቱን ለማንጻት ሁለት ወፎች፣ የጥድ እንጨት፣ ደማቅ ቀይ ድር እና ሂሶጵ ይውሰድ፡፡ 50 ከወፎቹ አንዱ ንጹህ ውሃ በያዘ በሸክላ ዕቃ ውስጥ ያርደዋል፡፡ 51 የጥድ እንጨት፣ሂሶጵደማቅ ቀይ ድር እና በህይወት ያለ ወፍ ይውድና በታረደው ወፍ ደም ውስጥ እና በንጹህ ውሃ ውስት ይነክራቸዋል፣ከዚያም ቤቱን ሰባት ጊዜ ይርጨው፡፡ 52 ቤቱን በወፉ ደምና በንጹህ ውሃ፣ በህይወት በሚገኘው ወፍ፣ በጥድ እንጨት፣በሂሶጵና በደማቅ ቀይ ድር ያነጻዋል፡፡ 53 በህይወት የሚገኘውን ወፍ ግን ከከተማ ውጭ ወደ ሜዳ ይለቀዋል፡፡ በዚህ መንገድ ቤቱን ያስተሰርያል፣ ቤቱም ንጹህ ይሆናል፡፡ 54 ለሁሉም አይነት ተላላፊ የቆዳ በሽታና እንዲህ ያለውን በሽታ ለሚያመጡ ነገሮች፣ እንዲሁም ለሚያሳክክ ህመም፣ 55 እንዲሁም ለልብስና ለቤት ብክለት፣ 56 ለእብጠት፣ ለሚያሳክክ ህመም፣ እና ለቋቁቻ፣ 57 በእነዚህ ሁኔታዎች እርኩስና ንጹህ የሚሆነውን ለመለየት ህጉ ይህ ነው፡፡”



Leviticus 14:1

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው ከቆዳ በሽታ ሲነጻ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

የመንጻቱ ቀን

ሰውየው በሥርዓቱ መሠረት ንጹህ እንደሆነ ካህኑ የሚያሳውቅበት ቀን ያመለክታል

እርሱም ወደ ካህኑ መወሰድ አለበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “አንድ ሰው ወደ ካህኑ እንዲወስደው ይገባል”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

Leviticus 14:3

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው ከቆዳ በሽታ ሲነጻ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ተላላፊ የቆዳ በሽታ

በዘሌዋዊያን 13:3 እነዚህን ቃላት እንዴት አንደተረጐሙ ይመልከቱ

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ንጹህ ወፎች

ሕዝቡ እንዲበላቸውና ለመሥዋዕትነት እንዲያቀርቡ የተፈቀዱ ወፎች በአካል ንጹህ ተብለዋል (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ደመቅ ያለ ቀይ ድር

“ቀይ ድር”

ሂሶጵ

ለመድኃኒትነት የሚጠቀሙት መልካም በዓዛ ያለው ዕጽ ነው (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Leviticus 14:6

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው ከቆዳ በሽታ ሲነጻ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

የታረደው ወፍ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ሰውየው ያረደው ወፍ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ንጹህ እንደሆነ ካህኑ ያስታውቀው

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ተቀባይነት ያለውና ሌሎች ሰዎች ሊነኩት የሚችሉት ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል፡፡ ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ

Leviticus 14:8

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው ከቆዳ በሽታ ሲነጻ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ካህኑ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ንጹህም ይሆናል

ሌሎች ሰዎች ሊነኩት የሚችሉት ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 14:10

እርሱ ያቅርብ

እዚህ “እርሱ” የሚነጻውን ሰው ያመለክታል::

እፍ

አንድ እፍ 22 ሊትር ነው:: መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች ይመልከቱ

ሎግ

አንድ ሎግ ዐ.31 ሊትር ነው::

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

Leviticus 14:12

ሎግ

አንድ ሎግ ዐ.31 ሊትር ነው:: መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎችን ይመልከቱ

በመሠዊያው ቦታ

ይህ ሀረግ የቀደመውን ሀረግ የሚገልጽና ካህኑ ጠባቱን የሚያርድበት ቦታ የሚናገር ነው

Leviticus 14:14

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ሎግ

አንድ ሎግ ዐ.31 ሊትር ነው:: መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎችን ይመልከቱ

ጥቂት ዘይት በእግዚአብሔር ፊት ይርጭ

በእግዚአብሔር መገኘት ጥቂት ዘይት ይርጭ

Leviticus 14:17

በእጁ ውስጥ ከቀረው ዘይት

በመዳፉ ውስጥ ከቀረው ዘይት

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

በእግዚአብሔር ፊት

በእግዚአብሔር መገኘት

Leviticus 14:19

የሚነጻውም ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ):: ሰውየውም ንጹህ ይሆናል

ንጹህም ይሆናል

ሌሎች ሰዎች ሊነኩት የሚችሉት ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 14:21

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው ከቆዳ በሽታ ሲነጻ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

አቅሙ ካልፈቀደለት

ለመግዛት ገንዘብ ከሌለው

ይወዘወዝ… ለእርሱ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ካህኑ ለእርሱ… ይወዘውዘው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

የእፍ አንድ አሥረኛ

የእፍ አንድ አሥረኛ 22 ሊትር ነው

ሎግ

አንድ ሎግ ዐ.31 ሊትር ነው:: (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎችን ይመልከቱ)

Leviticus 14:24

ሎግ

አንድ ሎግ ዐ.31 ሊትር ነው:: (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎችን ይመልከቱ)

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

Leviticus 14:26

አጠቃላይ መግለጫ

አንድ ሰው ከቆዳ በሽታ ሲነጻ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን ይናገራል፡፡

ጥቂት ዘይት… በእግዚአብሔር ፊት.. ይርጭ

ጥቂት ዘይት በእግዚአብሔር መገኘት ይርጭ:: በምን ላይ ካህኑ ዘይቱን እንደሚረጭ አልተገለጸም::

Leviticus 14:28

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

Leviticus 14:30

ይሠዋል

“ካህኑ ይሠዋል”

የሚነጻው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እርሱ የሚያነጻው ሰው”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ተላላፊ የቆዳ በሽታ

በዘሌዋዊያን 13፡3 እንዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ዐቅም ያነሰው

መደበኛ መሥዋዕት ለመግዛት በቂ ገንዘብ የሌለው ሰው እንዳሆነ ግልጽ በማድረግ ይተረጉሙ:: አት “በቂ ገንዘብ የሌለው ሰው” (ግምታዊ ዕውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 14:33

እናንተ በገባችሁ ጊዜ

እዚህ እናንተ የእስራኤልን ሕዝብ ያመለክታል (ሁለተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

አረንጓዴ ወይም ቀይ ምልክት ያለው ክፉ ደዌ

በዘሌዋዊያን 13:47 ይህን ቃል እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ርስት አድርጌ የሚሰጣቸው ምድር

“ርስት አድርጌ የሚሰጣቸው” በግሥ መልክ ሊተረጐም ይችላል አት “የሚትወርሱት ምድር” (ረቂቅ ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Leviticus 14:36

በቤት ውስጥ ያለ ምንም ነገር ርኩሰ አይሆንም

አንደ ካህኑ ቤቱ ርኩስ መሆኑን ካስታወቅ በቤቱ ውስጥ ያለው ሁሉም ነገር ርኩስ ይሆናል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “በቤት ውስጥ የቀረው ምንም ነገር ርኩስ መሆኑን ማስታወቅ አይገባውም”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ቤቱ ርኩስ ይሆናል

ሕዝቡ እንዲኖሩት ወይም እንዲነኩት ያለተገባ እንደሆነ እግዚአብሔር የተናገረው ቤት በአካል ርኩስ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

በግድግዳዎች አካል ክፍሎች

ክፉ ደዌው ከግድግዳዎች ላይኛው አካል ከፍል ባለፍ ሠርጾ የገባ እንደሆነ ካህኑ መርምሮ የሚወስንበት ማለት ነው

Leviticus 14:39

ክፉ ደዌው ከተገኘ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ክፉ ደዌውን ካገኙ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ርኩስ ሥፍራ

ሕዝቡ እንዳይሠፍር ወይም ለእግዚአብሔር ዓላማዎች የማይጠቅም እግዚአብሔር የተናገረው ሥፍራ በአካል ርኩስ ተብሎአል ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ

Leviticus 14:41

እርሱ ይፈልጋል

እዚህ እርሱ ካህኑን ያመለክታል

የተበከለው ውስጠኛው የቤቱ ግድግዳ በሙሉ ይፋቅ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ባለቤቱ የቤቱን ውስጠኛ ግድግዳዎችን ይፍቃል”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

የተበከለው ዕቃ ይፋቅ

ይህም ክፉ ደዌ የነካው ዕቃ ማለት ነው ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እነርሱ የሚፍቁት የተበከለው ዕቃ”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ርኩስ ሥፍራ

ሕዝቡ እንዳይሠፍር ወይም ለእግዚአብሔር ዓላማዎች የማይጠቅም እግዚአብሔር የተናገረው ሥፍራ በአካል ርኩስ ተብሎአል ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ

የተወገዱትም ድንጋዮች

ይህም ክፉ ደዌ የነካው ዕቃ ማለት ነው ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “እነርሱ ያስወገዱአቸው ድንጋዮች”፡፡ (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ሌላ ጭቃ ወስደው ይመርጉ

ድንጋዮችን በአድስ ጭቃ ይሸፍኑ

Leviticus 14:43

ቤቱ ውስጥ… እንደና ይመረጋል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ባለቤቱ ቤቱ ውስጥ ድንጋዮችንና የግድግዳዎችን ፍቅፋቂ ካስወገደ በኋላ አድስ ድንጋዮችን በጭቃ ይመርጋል፡፡” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ቤቱ ርኩስ ነው

ሰዎችን ለማኖር ያልተገባ ቤት በአካል ርኩስ ተብሎአል

Leviticus 14:45

ቤቱ ይፍረስ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ቤቱን ይፍርሱት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ድንጋዩ እንጨቱና ምርጊቱ በሙሉ ይወገድ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ድንጋዩን እንጨቱንና ምርጊቱን ያስወጡት/ያስወግዱት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ማንኛውም ሰው ቢገባበት ያ ሰው ርኩስ ይሆናል

ቤቱን በመግባቱ ምክንያት ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባውና ሰዎች የማይነኩት ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ፡፡

እስከ ማታ

ጸሐይ እስኪጠልቅ

Leviticus 14:48

ቤቱ ከተመረገ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ባለቤቱ በአዲስ ጭቃ ድንጋዮችን ከመረገ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ቤቱ ንጹህ መሆኑን ያስታውቅ

ሰዎችን ለማኖር የተገባ ቤት በአካል ንጹህ ተብሎአል

Leviticus 14:49

ዝግባ እንጨት ቀይ ድርና ሂሶጵ

በዘሌዋዊያን 14:4 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

የታረደው ወፍ ደም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ያረደው ወፍ ደም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

Leviticus 14:52

ቤቱንም ያንጻው

“ካህኑ በሥርዓቱ መሠረት ቤቱን ያንጻ”

ቤቱም ንጹህ ይሆናል

ሰዎችን ለማኖር የተገባ ቤት በአካል ንጹህ ተብሎአል:: (ዜይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 14:54

ተላላፊ የቆዳ በሽታ

በዘሌዋዊያን 13፡3 እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

ክፉ ለምጽ ደዌ

በዘሌዋዊያን 13፡47 ይህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

ችፍታ

በዘሌዋዊያን 13:6 ይህን ቃላት እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

ርኩስ ወይም ንጹህ

ሌሎች ሰዎች የማይነኩት ሰውና ዕቃዎች በአካል ርኩስ ተብለዋል እናም ሰዎች መንካት የሚችሉአቸው በአካል ንጹህ ተብለዋል:: (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)


Chapter 15

1 ያህዌ ሙሴንና አሮንን እንዲህ ሲል ተናገራቸው፣ 2 ‹ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ ብላችሁ ንገረቸው፣ ‹ማንም ሰው ከሰውነቱ የሚወጣ የሚመረቅዝ ፈሳሽ ሲኖርበት፣ ንጹኅ አይደለም፡፡ 3 ንጹኅ የማይሆነ ከሚመረቅዝ ፈሳሽ የተነሳ ነው፡፡ ከሰውነቱ የሚወጣ ፈሳሽ ቢቀጥል ወይም ቢቆም ንጹህ አይደለም፡፡ 4 የሚተኛበት አልጋ ሁሉ ንጹኅ አይሆንም፣ የሚቀመጥበት ነገር ሁሉ ንጹኅ አይሆንም፡፡ 5 አልጋን የነካ ሁሉ ልብሱን ይጠብ ሰውየውም በውሃ ይታጠብ፣ እስከ ምሽት ድረስ ንጹኅ አይደለም፡፡ 6 የሚመረቅዝ ፈሳሽ ያለበት ሰው በተቀመጠበት ማናቸውም ነገር ላይ የተቀመጠ ማንኛውም ሰው ልብሱን ይጠብ፣ እርሱም በውሃ ይታጠብ፣ እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ 7 የሚመረቅዝ ፈሳሽ ያለበትን ሰው አካል የነካ ማንኛውም ሰው ልብሱን ይጠብ፣ እርሱም በውሃ ይታጠብ፡፡ እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ 8 እንዲህ ያለ ፈሳሽ ያለበት ሰው ንጹኅ በሆነ ሰው ላይ ንጹኅ በሆነ ሰው ላይ ቢተፋ፣ ያ ሰው ልብሱን ማጠብና እርሱም በውሃ መታጠብ አለበት፣ እስከ ምሽት ንጹኅ አይደለም፡፡ 9 ፈሳሽ ያለበት ሰው የተቀመጠበት ማንኛውም ኮርቻ ንጹኅ አይደለም፡፡ 10 ከዚያ ሰው በታች ያለን ማንኛውንም ነገር የነካ እስከ ምሽት ንጹኅ አይደለም፣ እነዚያን ነገሮች የተሸከመ ማንም ሰው ልብሱን ይጠብ እርሱም በውሃ ይታጠብ፤ እስከ ምሽት ንጹኅ አይደለም፡፡ 11 እንዲህ ያለ ፈሳሽ ያለበት ማንም ቢሆን አስቀድሞ እጆቹን በውሃ ሳያጠራ ቢነካ፣ የተነካው ሰው ልብሱን ይጠብ እርሱም በውሃ ይታጠብ፣ እስከ ምሽት ንጹኅ አይደለም፡፡ 12 እንዲህ ያለ ፈሳሽ ያለበትን ሰው የነካ ማናቸውም አይነት የሸክላ ዕቃ ይሰበር፣ የእንጨት የተሰራ ማጠራቀሚያ ሁሉ በውሃ ይንጻ፡፡ 13 ፈሳሽ ያለበት ሰው ከፈሳሹ ሲነጻ ለመንጻቱ ለእራሱ ሰባት ቀናትን ይቁጠር፤ ከዚያ ልብሶቹን ይጠብ ሰውነቱን በምንጭ ውሃ ይታጠብ፡፡ ከዚያ ንጹህ ይሆናል፡፡ 14 በስምንተኛው ቀን ሁለት ርግቦች ወይም ሁለት ኖሶች ይውሰድና ወደ መገናኛ ድንኳን ያህዌ ፊት ይቅረብ፣ በዚያ ወፎቹን ለካህኑ ይስጥ፡፡ 15 ካህኑ አንዱን ለሀጢአት መስዋዕት እና ሌላውን የሚቃጠል መስዋዕት ያቅርባቸው፣ እናም ካህኑ ለሰውዬው ስለ ፈሳሹ ማስተሰርያ ያድርግ፡፡ 16 የማንንም ሰው የዘር ፈሳሽ ሳይታሰብ በድንገት ከእርሱ ቢወጣ፣ መላ ሰውነቱን በውሃ ይታጠብ፣ እስከ ምሽት ድረስ ንጹህ አይደለም፡፡ 17 ማናቸውም የዘር ፈሳሽ የነካ ልብስ ወይም ሌጦ በውሃ ይታጠብ፤ እስከ ምሽት ንጹኅ አይደለም፡፡ 18 አንዲት ሴትና አንድ ወንድ አብረ ቢተኙና ወደ እርሷ የዘር ፈሳሽ ቢተላለፍ ሁለቱም በውሃ ይታጠቡ፣ እስከ ምሽት ንጹኅ አይደሉም፡፡ 19 አንዲት ሴት የወር አበባ ሲፈሳት፣ ያለመንጻቷ ለሰባት ቀናት ይቀጥላል፣ እርሷን የነካ ሁሉ እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ 20 በወር አበባ ወቅት የምትተኛበት ማንኛውም ነገር ንጹህ አይደለም፤ እንደዚሁም የምትቀመጥበት ነገር ሁሉ ንጹኅ አይደለም፡፡ 21 አልጋውን የነካ ማንኛም ሰው ልብሱን ይጠብ እርሱም በውሃ ይታጠብ፣ ያሰው እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ 22 የተቀመጠችበትን ማናቸውንም ነገር የነካ ሁሉ ልብሱን ይጠብ እርሱም በውሃ ይታጠብ ያ ሰው እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ 23 በአልጋም ይሁን በማንኛም ነገር ላይ ብትቀመጥ የተቀመጠችበትን ነገር የነካ ሰው እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ 24 ከእርሷ ጋር የተኛ ንጹህ ያልሆነ ፈሳሽ ቢነካ፣ ለሰባት ቀናት ንጹህ አይደለም፡፡ የሚተኛበትም አልጋ ንጹህ አይደለም፡፡ 25 አንዲት ሴት ከወር አበባ ቀናት በኋላ ለብዙ ቀናት ደም መፍሰሱን ቢቀጥል፣ ይህም ከወር አበባ ጊዜያት በኋላ ፈሳሽ ቢኖርባት፣ ንጹኅ ባልሆነችባቸው ፈሳሽ ባለባት ጊዜያት ሁሉ፣ በወር አበባ ወቅት ላይ እንዳለች ሁሉ እርኩስ ይሆናል ንጹህ አይደለችም፡፡ 26 ደሟ በሚፈስባቸው ጊዜያት የምትተኛበት አልጋ ሁሉ በወር አበባ ወቅት እንደምትተኛበት እርኩስ ይሆናል፣ የምትቀመጥበት ነገር ሁሉ ልክ በወር አበባ ወቅት እንደሚሆነ ንጹህ አይደለም፡፡ 27 ደግሞም ከእነዚህ ነገሮች ማናቸንም የነካ ሁሉ ንጹህ አይደለም፤ ልብሶቹን ይጠብ እርሱም በውሃ ይታጠብ፤ እስከ ምሽት ድረስ ንጹህ አይደለም፡፡ 28 ነገር ግን ከደም መፍሰሳ ብትነጻ፣ ለራስዋ ሰባት ቀናትን ትቆጥራለች፣ እናም ከዚያ በኋላ ንጹኅ ናት፡፡ 29 በስምንተኛው ቀን ሁለት ርግቦች ወይም ሁለት ዋኖሶች ትወሰድና ወደ መገናኛው ድንኳን መግቢያ ለካህኑ ትስጥ፡፡ 30 ካህኑ አንዱን ወፍ ለሀጢአት መስዋእት ሌላውን ለሚቃጠል መስዋዕት ያቅርብ፣ ስለ ፈሳሽም እርኩሰት በያህዌ ፊት ያስተሰርይላታል፡፡ 31 የእስራኤል ሰዎች ከእርኩሰታቸው የምትይች እንደዚህ ነ፣ ይህ ከሆነ በመካከላቸ የምኖርበትን ቤተ መቅደሴን በማርከስ በእርኩሰታቸ አይሞቱም፡፡ 32 ከሰነቱ ፈሳሽ ለሚጣ፣ የዘረ ፈሳሹ ከእርሱ ለሚጣና ለሚያረክሰ ማንኛም ሰ ህግጋቱ እነዚህ ናቸ፡፡ 33 ለማንኛም በር አበባ ላይ ላለች ሴት፣ ከሰነቱ ፈሳሽ ለሚፈሰ ሰ ሁሉ፣ ንድም ይሁን ሴት፣ እንዲሁም ንጹህ ካልሆነች ሴት ጋር ለሚተኛ ንድ ህጉ ይህ ነ፡፡”



Leviticus 15:1

ከሰውነቱ የሚወጣ

የሰው አካል ክፍሎች የሚወጣ (See Euphemism/ንኣብነት ወይም ጸያፍ/አሳፋሪ አባበሎችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች የማይነኩት ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል(ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ይህ ርኩስ ነው

“አካሉ ርኩስ ነው”

Leviticus 15:4

ርኩስ ነው

ሰውየው የተኛበት አልጋ ወይም የተቀመጠበት ማንኛውም ነገር ሌሎች ሰዎች የማይነኩት በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

አልጋውን የሚነካ ማንኛውም ሰው ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እስከማታ

“ጸሐይ እስኪጠልቅ”

Leviticus 15:6

ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እስከማታ

“ጸሐይ እስኪጠልቅ”

የሚነካ ሰው

ማንኛውንም የአካል ክፍል የሚነካ

Leviticus 15:8

ንጹህ የሆነ ሰው

ሌሎች ሰዎች መንካት የሚችሉት ሰው በአካል ንጹህ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ኮርቻ

ኮረቻ በፈረስ ላይ ለመቀመጥ በጀርባው የሚቀመጥ ከቆዳ የተሥራ መቀመጫ ነው

ማንኛውም ኮሪቻ….ርኩስ ይሆናል

መንካት ያልተገባ እግዚአብሔር የተናገረው ማንኛውም ነገር በአካል ርኩስ ተብሎአል ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ

Leviticus 15:10

አጠቃላይ መረጃ

ቁስልን ለማስወገድ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴና አሮን መናገር ይቀጥላል

ያ ሰው

የቁስል ፈሳሽ ያለውን ሰው ያመለክታል

ርኩስ ነው

ሌሎች ሰዎች የማይነካው ሰው በአካል ርኩስ ተብሎአል፡፡ (ዜይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እስከማታ

“ጸሐይ እስኪጠልቅ”

ፈሳሽ ነገር የሚወጣው የነካው

ፈሳሽ ነገር የሚወጣው ሰው የነካው

የተነካው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል፡፡ አት፤ “ፈሳሽ ነገር በሚወጣው ሰው የተነካው ሰው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)::

ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው የሚነካውን የሸክላ ዕቃ ይስበሩት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው የሚነካውን ማንኛውንም የሸክላ ዕቃ ይስበሩት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የእንጨቱም ዕቃ ሁሉ በውሃ ይታጠብ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የእንጨቱንም ዕቃ ሁሉ አንድ ሰው በውሃ ይጠበው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 15:13

ከፈሳሹ ነገር ይነጻል

ከበሽታው እየገገመ ያለው ሰው በአካል ንጹህ እንደሆነ ተገልጾአል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ከፈሳሽ ነገር ይፈወሳል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር እና ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ንጹህም ይሆናል

ሌሎች ሰዎች መንካት የሚችለው ሰው በአካል ንጹህ እንደሆነ ተነገሮአል:: (ዘይቤያዊ አጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 15:16

እስከማታ ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች መንካት የሌለባቸው ሰዎችና ዕቃዎች በአካል ርኩስ ተብለዋል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እስከማታ ርኩስ

ጸሐይ እስኪትጠልቅ

ማንኛውም ልብስ በውሃ ይታጠብ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አንድ ሰው ዘር የነካውን ልብስ ወይም ቁርበት ሁሉ በውሃ ማጠብ አለበት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 15:19

ሴት ፈሳሽ ነገር ቢኖርባት …. በወር አበባዊ ጊዜ

ሁለቱም ከሴት ማዕጸን ደም የሚፈስስበትን ጊዜ ያመለክታሉ

መርገምዋ ይቀጥላል

“ንጹህ እንዳልሆነች ይቀጥላል”

ርኩስ ነው

ሌሎች ሰዎች መንካት የሌለባቸው ሰዎችና ዕቃዎች በአካል ርኩስ ተብለዋል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 15:21

መኝታዋ

ይህ የወር አበባ የሚፍስሳትን ሴት ያመለክታል

ያ ሰው ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች የማይነኩት ሰው በአካል ርኩስ ይባላል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 15:24

የመርገምዋ ወር አበባዋ ፈሳሽ

ንጹህ ያልሆነው ፈሳሽዋ ወይም ከማዕጸንዋ የሚወጣው ፈሳሽ

ርኩስ ነው

ሌሎች ሰዎች መንካት የሌለባቸው ሰዎችና ዕቃዎች በአካል ርኩስ ተብለዋል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 15:25

ልክ እንደወር አበባዋ ጊዜ ቢትሆን

ከመደበኛ የወር አበባዋ ጊዜ ውጪ ከማዕጸንዋ ደም የሚፈስሳት ከሆነ እንደወር አበባዋ ጊዜ ርኩስ ነች ማለት ነው::

እርስዋ ርኩስ ትሆናለች የሚነካትም ማንኛውም ሰው ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች መንካት የሌለባቸው ሰዎች በአካል ርኩስ ተብለዋል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

የምትቀመጥበትም ማንኛውም ነገር ርኩስ ይሆናል::

ሌሎች ሰዎች የማይነኩት ዕቃዎች በአካል ርኩስ ተብለዋል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)::

Leviticus 15:28

ነገር ግን እርስዋ

እዚህ “እርስዋ” የሚለው የወር አበባ ያላትን ሴት ነው::

ከደምዋ ፍሳሽ ንጹህ ትሆናለች

ከፍሳሽዋ እየተሻላት ያለች ሴት በአካል ንጹህ ተብላለች ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ከደምዋ ፍሳሽ እየተሻላት ያለች” (ዘይቤያዊ አገላለጽ እና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ንጹህ ትሆናለች

ሌሎች ሰዎች መንካት የሚችሉአት ሴት በአካል ንጹህ ተብላለች (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)::

ይዛ ትቀርባለች

ስለራስዋ ታቀርባለች

የደም ፈሳሽዋ ርኩሰት

ርኩስ የሚያደርጋት የደም ፍሳሽዋ

Leviticus 15:31

ይህም እስራኤላዊያንን ከሚያረክሱአቸው ነገር የሚትለዩበት ነው::

ሕዝቡን ከሚያረክሰው ነገር ስለመከላከል እግዚአብሔር የሚናገረው ሕዝቡን ከርኩሰት በርቀት እንደመጠበቅ ተገልጾአል:: “ርኩሰት” የተባለው ረቂቅ ስም እንደ “ርኩስ” ሊገለጽ ይችላል:: አት ይህ የእስራኤልን ሕዝብ ከርኩሰት ለመከላከሉበት ነው (ዘይቤያዊ አገላለጽ እና ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

ርኩስነታቸው

ሌሎች ሰዎች የማይነኩአቸውና ለእግዚአብሔር ዓላማ ተቀባይነት የሌላቸው ሰዎች በአካል ርኩስ ተብሎአል ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ

Leviticus 15:32

እነዚህ መመሪያዎች ናቸው

እነዚህ መደረግ የሚገባቸው ነገሮች ናቸው::

ርኩስ ያደርገዋል … ርኩስ ሴት

ሌሎች ሰዎች የማይነኩአቸው ሰዎች በአካል ርኩስ ተብለው ተገልጸዋል::

በወር አበባ ላይ ያለች

የወር አበባ የሚፈስሳት ወይም ከማዕጸንዋ ደም የሚፈስሳት


Chapter 16

1 ያህ እንዲህ ሲል ሙሴን ተናገረ፡ - ይህ የሆነ የአሮን ሁለቱ ልጆች ¨ደ ያህ«ከቀረቡና ከሞቱ በሀላ ነበር፡፡ 2 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለ፣ “ለ¨ንድምህ ለአሮን እንዲህ ብለህ ተናገረ፣ በፈለገ¬ ጊዜ ሁሉ በመጋረጃ ¬ስጠኛ ¨ዳለ ¨ደ ቅድስተ ቅዱሳኑ፣ በታቦቱ ላይ ወዳለ ወደ ማስተሰርያ ክዳን ፊት እንዳይቀርብ ንገረው፡፡ ይህንን ካደረገ፣ ይሞታል፣ ምክንያቱም እኔ በደመና በማስተሰርያ ክዳን ፊት እንዳይቀርብ ንገረው፡፡ ይህንን ካደረገ፣ ይሞታል፣ ምክንያቱም እኔ በደመና በማስተሰርያ ክዳን ላይ እገለጣለሁ፡፡ 3 ስለዚህም አሮን ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ መቅረብ ያለበት እንደዚህ ነው፡፡ ለሀጢአት መስዋዕት ወይፈን፣ ለሚቃጠል መስዋዕት አ¬ራ በግ ይዞ መግባት አለበት፡፡ 4 ቅዱሱን በፍታ ቀሚስ ይልበስ፣ እንዲሁም የበፍታ የስጥ ሱሪ ይልበስ፣ ደግሞም የበፍታ መጠምጠሚያ የበፍታ ቀሚስ ይልበስ፡፡ ቅዱሳኑ አልባሳት እነዚህ ናቸው፡፡ ሰውነቱን በውሃ ይታጠብና እነዚህን ልብሶች ይልበስ፡፡ 5 ከእስራኤል ሰዎች ጉባኤ ሁለት ወንድ ፍየሎችን ለሀጢአት መስዋዕት እንዲሁም አንድ አ¬ራ በግ ለሚቃጠል መስዋዕት ይውሰድ፡፡ 6 ከዚያም አሮን ለእራሱ ኮርማ¬ን ለኃጢአት መስዋዕት ያቅርብ፣ ይህም ለራሱና ለቤተሰቡ ማስተሰርያ ነው፡፡ 7 ቀጥሎም ሁለቱም ፍየሎች ወስዶ በመገናኛ¬ ድንኳን መግቢያ ላይ በያህዌ ፊት ያቁማቸው፡፡ 8 ከዚያ አሮን በሁለቱ ፍየሎች ላይ ዕጣ ይጣል፣ አንዱን ዕጣ ለያህዌ ሌላ¬ን ዕጣ ለሚለቀቀው ፍየል ይጣል፡፡ 9 ከዚያም አሮን ዕጣ ለያህ«የ¨ጣለትን ፍየል ያቀርባል፣ ያንን ፍየልም ለኃጢአት መስªዕት ያቀርበªል፡፡ 10 ለመለቀቅ ዕጣ የጣትን ፍየል ግን ወደ ምድረበዳ በመልቀቅ ለስርየት ከነህይ¨ት ለያህዌ መቅረብ አለበት፡፡ 11 ከዚያም አሮን ለእራሱ ኮርማን ለሀጢአት መስዋዕት ያቀርባል፡፡ ለራሱና ለቤተሰቡ ማስተሰርያ ማድረግ አለበት፣ ስለዚህ ኮርማን ለራሱ የሀጢአት መስዋዕት አድርጎ ይረዳ፡፡ 12 አሮን በያህዌ ፊት ከመሰዊያ የከሰል እሳት የሞላውን ማጠንት ይውሰድ፣ በእጆቹ ሙሉ የላመ ጣፋጭ ዕጣን ይያዝና እዚህንም ነገሮች ¨ደ መጋረጃ ¬ስጥ ይዞ ይግባ፡፡ 13 በዚያም በያህ«ፊት ዕጣኑን በእሳቱ ላይ ይጨምር፣ ከእጣኑ የሚ¨ጣ ጢስ በምስክሩ ላይ ያለ የማስተሰርያን ክዳን ይሸፍናል፡፡ እንዳይሞት ይህንን ያድርግ፡፡ 14 ከዚያም ከወይፈኑ ጥቂት ደም ይውሰድና በጣቱ በማስተሰርያ ክዳን ፊት ይርጭ ከደሙ ጥቂት ¨ስዶ በጣቱ ሰባት ጊዜ በማስተሰርያ ክዳን ፊት ይርጭ፡፡ 15 ከዚያም ለህዝቡ ኃጢአት የኃጢአት መስªዕት ፍየሉን ይረድና ደሙን ¨ደ መጋረጃ ¬ስጥ ይዞ ይግባ፡፡ በዚያም በኮርማ ደም እንዳደረገ ሁሉ ያድርግ በማስተሰርያ¬ ክዳን ላይ ደሙን ይርጭ ከዚያም በማስተሰርያ¬ ክዳን ፊት ይርጭ፡፡ 16 በእስራኤል ህዝብ ያልተቀደሱ ተግባራት፣ በአመጻቸ¬ና በኃጢአቶቻቸ¬ ሁሉ ምክንያት ለተቀደሰ ስፍራ ማስተሰርያ ያድርግ፡፡ ንጹህ ያልሆኑ ተግባሮቻቸ¬ በታዩ ጊዜያት፣ ያህ በመካከላቸ¬ ለሚያድርበት ለመገናኛ¬ ድንኳንም ይህን ያድርግ፡፡ 17 አሮን ለማስተሰርይ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን በሚገባበት ሰዓትና እንዲሁም ለእርሱ፣ ለቤተሰቡና ለእስራኤል ጉባኤ ሁሉ ማስተሰርዩን እስከሚጨርስ ድረስ ማንም ሰው በመገናኛው ድንኳን ውስጥ አይገኝም፡፡ 18 በያህ«ፊት ወዳለ መሰዊያ ይሂድና መሰዊያን ያስተሰርይ፣ ከኮርማ ደም ጥቂት እንዲሁም ከፍየሉ ደም ጥቂት ይ¬ስድና በመሰዊያ ዙሪያ ባሉ ቀንዶች ሁሉ ¬ስጥ ያስነካ፡፡ 19 መሰዊያዉን ንጹህ ካልሆነ የእስራኤል ሰዎች ድርጊቶች ለማንጻትና ለያህዌ ለመለየት በላዩ ካለ ጥቂት ደም ወስዶ በጣቱ ሰባት ጊዜ ይርጭ፡፡ 20 ቅድስተ ቅዱሳኑን፣ የመገናኛን ድንኳንና መሰዊያን ማስተሰርያ¬ን ሲጨርስ በህይወት የሚገኘ¬ን ፍየል ያቅርብ፡፡ 21 አሮን ህይወት ባለው ፍየል ላይ ሁለቱንም እጆቹን ይጫንና የእስራኤልን ህዝብ በደልን ሁሉ፣ አመጻቸውን ሁሉ፣ እና ሀጢአታቸውን ሁሉ በላዩ ላይ ይናዘዝበት፡፡ ከዚያም ያንን ሃጢአተኛነት በፍየሉ ራስ ላይ አድርጎ ፍየሉን ወደ በረሃ ለመስደድ ኃላፊነት ባለበት ሰው አማካይነት ወደ በረሃ ያባው፡፡ 22 ፍየሉ የሰ­ቹን በደል ሁሉ ይሸከምና ገለልተኛ ¨ደ ሆነ ስፍራ ይሄዳል፡፡ በበረሃ ስፍራም፣ ሰ¬ዬ¬ ፍየሉን ይለቀªል፡፡ 23 ከዚያም አሮን ወደ መገናኛ ድንኳን ይመለስና ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ከመሄዱ አስቀድሞ የለበሰን የበፍታ ልብሶች ያወልቃል፣ እነዚያን ልብሶችም በዚያ ስፍራ ያስቀምጣቸዋል፡፡ 24 በተቀደሰ ስፍራ ሰውነቱን በውሃ ይታጠብ፣ ከዚያም የዘወትር ልብሱን ይልበስ፣ ከዚያም ወጥቶ የራሱን የሚቃጠል መስዋዕቱን የህዝቡን የሚቃጠል መስዋዕት ያቅርብ፤ በዚህ መንገድ ለራሱና ለህዝቡ ማስተሰርያ ያቀርባል፡፡ 25 በመሰዊያ ላይ የኃጢአት መስዋዕቱን ስብ ያቃጥል፡፡ 26 የሚሰደደውን ፍየል የለቀቀው ሰው ልብሶቹንና ሰውነቱን ይታጠብ፣ ከዚያ በኋላ ወደ ሰፈር መመለስ ይችላል፡፡ 27 በተቀደሰው ስፍራ ለማስተሰርያው ደማቸው የቀረበው የኃጢአት መስªዕቱ ኮርማ እና የኃጢአት መስªዕቱ ፍየል ከሰፈር ውጭ ይውስዳቸው። በዚያም ቆዳቸውን፣ ስጋቸውንና ፈርሳቸውን ያቃጥላFቸው፡፡ 28 እነዚህን የእንስሳውን ክፍሎች የሚያቃጥለው ሰው ልብሶቹንና ሰውነቱን በውሃ ይታጠብ፣ ከዚያ በኋላ፣ ወደ ሰፈር መመለስ ይችላል፡፡ 29 በሰባተኛው ወር፣ በወሩ በአስረኛው ቀን ራሳችሁን ትሁት ታደርጋላችሁ ስራም አትሰሩበትም ለእናንተም ሆነ ለመጻተኛው ይህ ሁልጊዜም መታሰቢያ ይሆናል፡፡ 30 ይህ የሚሆነው በዚህ ዕለት በያህዌ ፊት ቅዱስ ትሆኑ ዘንድ ከኃጢአቶቻችሁ ሁሉ እንድትነጹ ማስተሰርያ ስለሚደረግላችሁ ነው፡፡ 31 ይህ ለእናንተ ክቡር ሰንበት ዕረፍት ነው፣ ራሳችሁን ትሁት ማድረግ አለባችሁ ምንም ስራ አትስሩበት፡፡ይህ በእናንተ መሀል ሁልጊዜም መታሰቢያ ነው 32 ሊቀ ካህኑ፣ በአባቱ ስፍራ ሊቀካህን ሊሆን የሚቀባውና የሚሾመው፣ ይህን ማስተሰርያ ማስፈጸምና ቅዱስ የሆነውን የበፍታ ልብሶች መልበስ አለበት፡፡ 33 ለቅድስተ ቅዱሳኑ፣ ለመገናኛው ድንኳንና ለመስዋዕቱ፣ ማስተሰርያ ያደርጋል፤ እንደዚሁም ለካህናቱና ለጉባኤው ሰዎች በሙሉ ማስተሰርያ ያደርጋል፡፡ 34 "ይህ ለእናንተ ሁልጊዜም መታሰቢያ ይሆናል፣ ለእስራኤል ሰዎች ለኃጢአቶቻቸው ሁሉ ማስተሰርያ ለማቅረብ ይህ በየአመት አንድ ጊዜ ይደረግ፡፡” ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው እንዲሁ ተደረገ፡፡



Leviticus 16:1

የአሮን ሁለቱ ልጆች

ናዳብና እብዩድ ይመለከታል እግዚአብሔር ያልተቀበለውን እሳት በማቅረባቸው ምክንያት ሞተዋል ዘሌዋዊያን 1ዐ: 1-2 ይመልከቱ::

Leviticus 16:3

ስለዚህ እዚህ እንዲህ

“ይህም እንዲህ”

የውስጥ ልብስ ወይም የውስጥ ሱሪ

“ከውጨኛው ልብስ ውስጥ በሰውነት ላይ የሚያርፍ ከበፍታ የተሠራ ልብስ”

መቀነት

“በወገብ ወይም በደረት ዙሪያ የሚታጠቅ ከቀጭን ረጅም ጨርቅ የተሠራ”

መጠምጠሚያ

“ከጨርቅ ክፍልፋዮች የተሠራ ጭንቅላት መሸፈኛ ሻሽ”

ከእስራኤል ማኀበረሰብ

“ከእስራኤል ጉባዔ”

Leviticus 16:6

የኃጢአት መሥዋዕት ስለራሱ

ስለራሱ የኃጢአት መስዋዕት

Leviticus 16:8

የሚለቀቅ ፍዬል

የሚለቀቀው ፍዬል አሮንም አንድ ሰው ፍዬሉን ወደ ምድረ በዳ እንዲለቅቀው ያደርጋል

ዕጣው የሆነበት ወይም የወደቀበት

ዕጣው የመደበው

ነገር ግን ፍዬሉ በሕይወት በእግዚአብሔር ፊት መቅረብ አለበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ነገር ግን አሮን ፍዬሉን በሕይወት በእግዚአብሔር ፊት ማቅረብ አለበት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 16:11

አጠቃላይ መረጃ

በማስተሠረያ ቀን አሮን ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ወይፈኑን ይረድ

በኋላ በመሠዊያው መክደኛ ላይ ለመርጨት አሮን የወይፈኑን ደም በሳኀን ይያዝ የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 16:12

ጥና

ካህናት የሚጠቀሙት የእሳትና የዕጣን መያዣ

መልካም በዓዛ ያለው ዕጣን

መልካም በዓዛ የሚያሸት ዕጣን ይህ የዕጣኑን ሽታ ያመለክታል እንጂ ጣፋጭነት አይደለም

Leviticus 16:14

የወይፈኑ ደም

ይህ በዘሌዋዊያን 16:11 እንደተገለጸው አሮን በሳህን የያዘው ደም ነው::

በጣቱ ይርጭ

ደሙን ለመርጨት ጣቱን ይጠቀም

በሥርየቱ መክደኛ ትይዩ

በመክደኛው ላይ ደም ያድርግ ወይም ይርጭ እንዲሁ ደግሞ ወደ ቅዱሳነ ቅዱስ እንደገባ ከፊት ለፊቱ በመክደኛው ጐን ይርጨው

በሥርየቱ መክደኛ ፊት

ሁኔኛ ትርጉሞች: 1) ከሥርየቱ መክደኛ በታች በደረት አካባቢ 2) በሥርየቱ መክደኛ ፊት በመሬት

Leviticus 16:15

አጠቃላይ መረጃ

በማስተሠረያ ቀን አሮን ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ደሙን በስርየቱ መክደኛ ላይ እንዲሁም በመክደኛው ትይዩ ይርጭ

አሮን በወይፈኑ ደም እንዳደረገው ሁሉ ደሙን ይርጨው የቀደሙ ሕጐችን በዘሌዋዊያን 16:14 እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ከእስራኤል ሕዝብ ርኩሰታቸው የተነሣ ለቅድስተ ቅዱሳኑ ያስተሠርይለታል

የእስራኤል ኃጢአት ቅድስተ ቅዱሳኑን አርክሶአል

ርኩስ ድርጊቶች…አመጽ …ኃጢአት

እነዚህ ቃላት በመሠረቱ አንድ ናቸው ሰዎች ሁሉ ዓይነት ኃጢአቶች እንደሠሩ አበክረው ያሳያሉ

ርኩስ ድርጊቶች

ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት እንዳይኖር የሚያደርጉ ኃጢአታዊ ድርጊቶች ርኩስ ድርጊቶች ተብለዋል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

በርኩሰት ድርጊቶቻቸው መካከል

“ርኩሰት ድርጊቶቻቸው” የሚለው ሀረግ ኃጢአታዊ ድርጊቶችን የሚፈጽሙ ሰዎችን ያመላክታል (See Metonymy/ምትክ ተመሳሳይ አባባሎች ይመልከቱ)

Leviticus 16:17

በእግዚአብሔር ፊት ወዳለው መሠዊያ ይምጣ

ይህ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የሚገኝ የመሥዋዕት መሠዊያ ነው

ለመሠዊያው ያስተሠርይለት

እንደ ቅዱስ ቦታና መገናኛ ድንኳን መሠዊያው ከሰዎች ኃጢአት የተነሣ ርኩስ ይሆናል

የመሠዊያው ቀንዶች

በመሠዊያው ማዕዘናት ያሉ ቅርጾች ይህም የመሠዊያው ማዕዘናት ያመለክታል:: እንደ በሬ ቀንዶች የተቀረጹ ናቸው:: በዘሌዋዊያን 4:7 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ለማንጻት

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች መጠቀሚያ የሚገባው መሠዊያ ንጹህ እንደሆነ ተገልጾአል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔርም ይለዩት ከእስራኤልም ሕዝብ ርኩስ ተግባራት ያርቁት

ለእግዚአብሔር የተለየው መሠዊያ ከሕዝቡም ኃጢአት አንደተለየ ተደርጐ ተነግሮአል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ርኩስ ድርጊቶች

በእግዚአብሔር ፊት ሰዎች ተቀባይነት እንዳይኖራቸው የሚያደርጉ ኃጢአታዊ ድርጊቶች ርኩስ ድርጊቶች ተብለው ተነግረዋል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 16:20

በሕይወት ያለውን ፍዬል ያቅርበው

ይህ ፍዬል በዘለዋዊያን 16:1ዐ ላይ የሚለቀቅ ፍዬል ተብሎአል::

በላዩ ላይ ይናዘዝበት

በፍዬሉ ላይ ይናዘዝበት

ኃጢአታቸውን በፍዬሉ ራስ ላይ ያድርግ

እዚህ የአሮን ድርጊቶች ያ ፍዬል የበደላቸውን ቅጣት እንደሚሸከም ዓይነት የሕዝቡን ኃጢአት ወደ ፍዬሉ የማስተላለፍ ምልክት ናቸው:: (ምልክታዊ ድርጊቶችን ይመልከቱ)

ክፋት…. አመጽ…. ኃጢአት

እነዚህ ሁሉ በመሠረቱ ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: ሕዝቡ የፈጸመውን ማንኛውንም ኃጢአት አሮን ይናዘዛል::

Leviticus 16:23

የበፍታ ልብሶችን አውልቆ

እነዚህ አሮን ወደ ቅድስተ ቅዱሰኑ በሚገባበት ጊዜ የሚለብሱአቸው ልዩ ልብሶች ናቸው::

በተቀደሰውም ሥፍራ ሰውነቱን በውሃ ይታጠብ

እዚህ “ቅዱስ ሥፍራ” የመገናኛ ድንኳን አያመለክትም:: ይህ ሰውነቱን እንዲታጠብ የተለየ ልዩ ሥፍራ ነው::

የዘወትር ልብሱንም ይልበስ

እነዚህ ለመደበኛ ተግባራት አሮን የሚለብሱአቸው ልብሶች ናቸው፡፡

Leviticus 16:25

ያቃጥል

“አሮን ያቅጥል”

የሚለቀቀውን ፍዬል የወሰደው ሰው ልብሱን ይጠብ ሰውነቱንም በውሃ ይታጠብ

የሕዝቡን ኃጢአት የተሸከመውን የሚለቀቀውን ፍዬል ስለነካ ሰውየው ርኩስ ነው

የሚለቀቀው ፍዬል

“ተለቅቆ የሚሄድ ፍዬል” በዘሌዋዊያን 16:8 ይህን እንዴት አንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Leviticus 16:27

ደማቸው የገባው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መልክ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አሮን ያገባቸው ደማቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ተሸክመው ተወስደው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አንድ ሰው ተሸክሞ ይውሰድ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ቁርበታቸው

ቈዳቸው ወይም የእነርሱ ቈዳ፤ እዚህ “እነርሱ” ወይፈኑንና ፍዬሉን ያመለክታል::

Leviticus 16:29

ለእናንተ

እናንተ የሚለው ቃል ብዙና የእስራኤልን ሕዝብ የሚያመለክት ነው:: (የሁለተኛ ሰው አገላለጾች ይመልከቱ)

በሰባተኛው ወር በአሥረኛው ቀን

ይህ በዕብራይጥ የቀን መቁጠሪያ ሰባተኛ ወር ነው አሥረኛው ቀን በምዕራባዊያን አቆጣጠር መስከረም ማገባደጃ ወይም መጨረሻ አካባቢ ነው:: (የዕብራይጥ ወራትንና መደበኛ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ሥርየት ይደረግላችኋል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አሮን ሥርየት ያደርግላችኋል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ያነጻችኋል ….ስለዚህ ትነጻላችሁ

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ተቀባይነት ያሉአቸው ሰዎች ንጹህ ተብለዋል::

ይህች የፍጹም ዕረፍት ሰንበት ናት

ይህ በየሳምንቱ የሚያከብሩት የሰንበት ቀን አይደለም:: በሥርየት ቀን የሚደረግ ልዩ ሰንበት ነው::

Leviticus 16:32

የተቀባና የተሾመ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እነርሱ የሚቀቡትና የሚሾሙት ሰው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በአባቱ ምትክ

ሊቀ ካህን ሲሞት ከልጆቹ አንዱ ይተካዋል::

የተቀደሰው በፍታ ልብስ

ቅድስተ ቅዱሳን በሚገባበት ጊዜ ሊቀ ካህኑ የሚለብሱአቸው ልዩ ልብሶች ናቸው

ለማኀበረሰቡ ሁሉ

“ለእስራኤል ሕዝብ ሁሉ”

Leviticus 16:34

አጠቃላይ መረጃ

በማስተሠረያ ቀን ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይፈጽማል

እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘ እንዲሁ አደረገ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እናም ሙሴ እግዚአብሔር እንዳዘዘው አደረገ” ወይም “እናም አሮን እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘው አደረገ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)


Chapter 17

1 እንዲህ ሲል ሙሴን ተናገረው፣ 2 አሮንና ልጆቹን እንዲሁም የእስራኤል ህዝብ ሁሉ እንዲህ በላቸው፡፡ ያህዌ ያዘዘውን ንገራቸው፡፡ 3 “ከእስራኤል ሰዎች መሀል ማንም ለመስዋዕት በሰፈር ውስጥ ወይም ከሰፈር ውጭ በሬ፣ በግ፣ ወይም ፍየል ያረደ ሰው፣ 4 ወደ መገናኛው ድንኳን መግቢያ በመቅደሱ ፊት ለያህዌ መስዋዕት ለማድረግ ባመጣው ውሃ ያ ሰው ስላፈሰሰው ደም በደለኛ ነው” ደም አፍስሷልና ያ ሰው ከህዝቡ መሃል ተለይቶ ይጥፋ፡፡ 5 የዚህ ትእዛዝ ዓላማ የእስራኤል ሰዎች ለያህዌ በሜዳ ላይ የሚያቀርቧቸውን መስዋዕቶች ወደ ካህናት ለያህዌ የህብረት መስዋዕት አድርገው በመገናኛው ድንኳን መግቢያ እንዲያቀርቡ ነው፡፡ 6 ካህኑ የመስዋዕቱን ደም በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ በያህዌ መሰዊያ ላይ ይረጫል፤ ስቡን ለያህዌ ጣፋጭ ማዕዛ አድርጎ ያቃጥለዋል፡፡ 7 ሕዝቡ ከእንግዲህ መስዋዕቱን ለጣኦት አይሰዋ፣ እንዲህ ያለው ተግባር ምንዝርና ነው፡፡ ይህ በትወልዶቻቸው ሁሉ ቋሚ መታሰቢያ ይሆናል፡፡ 8 እንዲህ በላቸው፣ “ማንኛውም እስራኤላዊ፣ ወይም ማንኛውም በእነርሱ መሀል የሚኖር መጻተኛ፣ የሚቃጠል መስዋዕት የሚሰዋ ወይም መስዋዕት የሚያቀርብ 9 እና ለያህዌ ለመሰዋት ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ የማያመጣው ያ ሰው ከህዝቡ ተለይቶ ይጥፋ፡፡ 10 ደግሞም ከእስራኤል አንዱ፣ ወይም በእነርሱ መሀል ከሚኖር መጻተኛ አንዱ፣ ደም ቢበላ፣ ፊቴን ከዚያ ሰው አስቆጣለሁ፣ ማንንም ደም የሚበላን ሰው ከህዝቡ መሃል አጠፋዋለሁ፡፡ 11 የእንስሳ ህይወቱ በደሙ ውስጥ ነው፡፡ በመሰዊያ ላይ ማስተሰርያ ይሁናችሁ ዘንድ ደሙን ለሕይወታችሁ ሰትቻችኋለሁ፣ ምክንያቱም ማስተሰርያ የሚሆነው ደም ነው፣ ለሕይወት ስርየት የሚያስገኘው ደም ነው፡፡ 12 ስለዚህም ለእስራኤላውያን ከመሀላችሁ ማንም ደም አይብላ እላለሁ፣ በመሀላችሁ የሚኖር ማንም ሙያተኛም ቢሆን ደም አይብላ፡፡ 13 ከእስራኤል ሰዎች መሀል ማንም ቢሆን፣ ወይም በእነርሱ መሃል የሚኖር ማንኛውም መጻተኛ፣ የሚበላ እንስሳ ቢያርድ ወይም ወፍ ቢያጠምድ ደሙን ያፍስና በአፈር ይሸፍነው፡፡ 14 የእያንዳንዱ ፍጥረት ነፍስ ደሙ ነውና፡፡ ስለዚህም ነው ለእስራኤላውያን፣ የማንኛውም ፍጥረት ደም አትብሉ፣ የእያንዳንዱ ሕያው ፍጥረት ሕይወት ደሙ ነው፡፡ ማንም ይህን የሚበላ ተቆርጦ ይጥፋ” ብዬ የተናገርኩት፡፡ 15 እያንዳንዱ የሞተ፣ ወይም በዱር አውሬ የተዘነጠለ እንስሳ የበላ ሰው የአገር ተወላጅ ይሁን በመሀላችሁ የሚኖ መጻተኛ ልብሶቹን ይጠብ፣ እርሱም በውሃ ይታጠብ፣ እስ ምሽት ድረስ ንጹህ አይሆንም፡፡ ከዚያ ንጹህ ይሆናል፡፡ 16 ነገር ግን ልብሱን ባያጥብ ወይም ሰውነቱን ባይታጠብ፣ በበደሉ ተጠያቂ ነው፡፡



Leviticus 17:1

በእግዚአብሔር ማደሪያ ፊት

በታቦቱ ፊት

ያ ሰው ከሕዝቡ ተቆርጦ ይወገድ ወይም ተለይቆ ይጥፋ

ከኀብረተሰቡ የሚገለል ሰው የልብስ ጨርቅ ወይም የዛፍ ቅርንጫፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ እንደሚቆረጥ ተደርጐ ተነግሮአል:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: በዘሌዋዊያን 7:2ዐ ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልኩቱ:: አት፤ “በሕዝቡ ዘንድ ያ ሰው እንዲኖር አይገባም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 17:5

ለመሠዋት ወደ ካህኑ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ካህኑም መሥዋዕት አድርጐ እንዲያቀርባቸው ወደ ካህኑ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 17:7

ላመነዘሩባቸው

ስህተት አማልዕክትን በማምለክ ለእግዚአብሔር ታማኝ ያልሆነው ሕዝብ በማመንዘር ባለቤቱን እንደካደ ሰው እንደሆነ ተገልአል አት፡ ለእግዚአብሔር ታማኝ ላልሆኑበት፤ (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ለእነርሱና ከእነርሱ በኋላ ለሚነሣው ትውልድ ይህ የዘላለም ሥርዓት

በዘሌዋዊያን 3: 17 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Leviticus 17:8

ያ ሰው ከሕዝቡ ተለይቶ ይጥፋ

የሰውየው ከማኀበረሰቡ መገለሉ አንድ ቢጣሽ ጨርቅ ከልብስ ወይም ቅርንጫፍ ከዛፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ እንደተቆረጠ ተደርጐ ተነግሮአል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ያ ሰው በሕዝቡ መካከል መኖር የለበትም” ወይም “ያ ሰው ከሕዝቡ መለየት አለበት” ( ዘይቤያዊ አገላለጽና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 17:10

በዚያ ሰው ላይ ፊቴን አከብድበታለሁ

ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር “በጥብቅ እንደወሰነ” ይገልጻል:: አት: “ያን ሰው ለመቃወም በአእምሮዬ ወስኛለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ፊቴን ላከብድበት

“በቁጣ ሊገናኘው”

ከሕዝቡ ለይቼ እቆርጠዋለሁ/ አጠፋዋለሁ

የሰውየው ከማኀበረሰቡ መገለሉ አንድ ቢጣሽ ጨርቅ ከልብስ ወይም ቅርንጫፍ ከዛፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ እንደተቆረጠ ተደርጐ ተነግሮአል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ያ ሰው በሕዝቡ መካከል መኖር የለበትም” ወይም “ያ ሰው ከሕዝቡ መለየት አለበት” ( ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

የፍጡር ሕይወት በደሙ ነውና … ሕይወት ሥርየት የሚያስገኝ

ይህም ማለት ደም ሕይወት ስለሆነ እግዚአብሔር ደምን ተጠቅሞ የሰዎችን ኃጢአት ያስተሠርያል:: ይህ የተለየ ዓላማ ስላለው ሰዎች ደምን መብላት አይገባቸውም

Leviticus 17:12

“እኔ” እላለሁ

እዚህ “እኔ” ያህዌን ያመለክታል

ከእናንተ ማንም ደም አይብላ

“ከእናንተ ማንም ደም ያለበትን ሥጋ አይብላ”

ያ ሊበላ ይችላል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ያ እንዲበሉ እኔ የተናገርሁት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ደሙን አፈር ያልብሰው

“ደሙን የአፈር ብናኝ ያልብሰው”

Leviticus 17:14

የማንኛውም ፍጡር ሕይወት ደሙ ነውና

ይህም ማለት ደም ፍጡር በሕይወት እንዲኖር ያደርጋል የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት: “ከደሙ የተነሣ እያንዳንዱ ፍጡር በሕይወት ሊኖር ይችላሉ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የበላው ሰው ሁሉ ተለይቶ ይጥፋ

የሰውየው ከማኀበረሰቡ መገለሉ አንድ ቢጣሽ ጨርቅ ከልብስ ወይም ቅርንጫፍ ከዛፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ እንደተቆረጠ ተደርጐ ተነግሮአል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ደምን የሚበላ ማንኛውም ሰው በሕዝቡ ዘንድ መኖር የሌበትም” ወይም “ደም የሚበላውን ሰው ከሕዝቡ መለየት አለባችሁ” (ዘይቤያዊ አገላለጽና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 17:15

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር መናገሩን ይቀጥላል

አውሬ የዘነጠለውን

በአውሬ የተገደለው እንስሳ አውሬዎች አንሰሳውን ዘነጣጥለው እንደከፋፈሉት ተነግሮአል፡፡ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አውሬዎች የገደሉት” (ዘይቤያዊ አገላለጽና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የሀገር ተወላጅ

“እስራኤላዊ”

ርኩስ ይሆናል …. ከዚያም ርኩስ ይሆናል

ሌሎች ሰዎች ሊነኩት የማይችሉአቸው ሰው ርኩስ ተብሎአል እናም ሌሎች ሰዎች መንካት የሚችሉአቸው ሰው ንጹህ ተብሎአል::(ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እስከማታ

“ጸሐይ እስኪጠልቅ”

በደሉን ይሸከማል

የሰውየው በደል አንድን ግዑዝ ዕቃ ሰው እንደተሸከመ ተደርጐ ተነግሮአል:: እዚህ “በደል” የሚለው ቃል ለበደሉ የሚሰጠውን ቅጣት ያመለክታል:: አት: ያም እርሱ ለበደሉ ተጠያቂ ነው ወይም ስለ ኃጢአቱ እቀጣዋለሁ:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ወይም ምትክ ተመሳሳይ አባባሎችን ይመልከቱ)


Chapter 18

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ ብለህ ንገራቸው፣ “እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 3 እኔ በማስገባችሁ ምድር፤ ቀድሞ ትኖሩበት በነበረው በግብጽ የነበሩ ሰዎች ያደርጓቸው የነበሩ ነገሮችን አታድርጉ፣ ደግሞም በከነአን ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ያደርጓቸው የነበሩ ነገሮችን አታድርጉ፡፡ የእነርሱን ልምዶች አትከተሉ፡፡ 4 እናንተ መፈጸም ያለባችሁ የእኔን ህጎች ነው መጠበቅ ያለባችሁ የእኔን ትዕዛዛት ነው፣ ስለዚህም በእነርሱ ትኖራላችሁ፣ ምክንያቱም እኔ አምላካችሁ ያህዌ ነኝ፡፡ 5 ስለዚህም እኔን ትዕዛዛትና ህጎች ትጠብቀላችሁ፡፡ አንድ ሰው እነዚህን ቢጠብቅ፣ በእነርሱ ምክንያት በህይወት ይኖራል፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 6 ማንም ሰው ከቅርብ ዘመዱ ጋር አይተኛ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 7 ከእናትህ ጋር በመተኛት አባትህን አታዋርድ፡፡ እርሷ እናትህ ናት! እርሷን ማዋረድ የለብህም፡፡ 8 ከአባትህ ሚስት ከየትኛዋም ጋር አትተኛ፤ አባትህን በዚያን አይነት ማዋረድ የለብህም፡፡ 9 የአባትህ ልጅ ወይም የእናትህ ልጅ ብትሆን በቤት ውስጥ አብራህ ብታድግ ወይም ርቃ ብታድግም ከየትኛዋም እህትህ ጋር አትተኛ፡፡ 10 ከወንድ ልጅህ ሴት ልጅ ጋር ወይም ከሴት ልጅህ ሴት ልጅ ጋር አትተኛ፡፡ ይህ እፍረት ይሆንብሃል፡፡ 11 ከአባትህ ከተወለደች ከእንጀራ እናትህ ሴት ልጅ ጋር አትተኛ፡፡ እህትህ ናት፣ እናም ከእርሷ ጋር መተኛት የለብህም፡፡ 12 ከአባትህ እህት ጋር አትተኛ፡፡ ለአባትህ የቅርብ ዘመድ ናት፡፡ 13 ከእናትህ እህት ጋር አትተኛ፡፡ ለእናትህ የቅርብ ዘመድ ናት፡፡ 14 ወንድም ከሚስቱ ጋር በመተኛት አታዋርደው” ለዚያ ተግባር ወደ እርሷ አትቅረብ፣ አክስትህ ናት፡፡ 15 ከምራትህ ጋር አትተኛ፡፡ የወንድ ልጅህ ሚስት ናት፣ ከእርሷ ጋር አትተኛ፡፡ 16 ከወንድምህ ሚስት ጋር አትተኛ፣ በዚህ መንገድ አታዋርደው፡፡ 17 ከአንዲት ሴትና ከልጇ ጋር ወይም ከወንድ ልጇ ሴት ልጅ ጋር ወይም ከሴት ልጇ ሴት ልጅ ጋር አትተኛ፡፡ እነርሱ ለእርሷ የቅርብ ዘመዶች ናቸው፣ እናም ከእነርሱ ጋር መተኛት ጸያፍ ነው፡፡ 18 የሚስትህን እህት ሁለተኛ ሚስት አድርገህ አታግባ፤ ሚስትህ በህይወት ሳለች ከእህቷ ጋር አትተኛ፡፡ 19 አንዲት ሴት በወር አበባዋ ወቅት ላይ ሳለች አብረሃት አትተኛ፡፡ በዚያን ጊዜ ንጹኅ አይደለም፡፡ 20 ከጎረቤትህ ሚስት ጋር አትተኛ፣ በዚህ መንገድ ራስህን አታርክስ፡፡ 21 ከልጆችህ አንዳቸውንም በእሳት ውስጥ እንዲያልፉ አትስጥ፣ በዚህ ድርጊት ለሞሎክ መስዋዕት አድርህ ትሰጣቸዋለህ፣ የአምላክህን ስም ማቃለል የለብህም፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 22 ከወንዶች ጋር ከሴት ጋር እንደምትተኛው አትተኛ፡፡ ይህ ጻያፍ ነው፡፡ 23 ከማናቸውም እንስሳ ጋር አትተኛ ራስህን አታርክስ፡፡ ማንም ሴት ከማናቸውም እንስሳ ጋር መተኛት የለባትም፡፡ ይህ አስጸያፊ ወሲብ ነው፡፡ 24 ከእነዚህ መንገዶች በየትኛውም ራስህን አታርክስ፣ ከአንተ አስቀድሞ ያባረርኳቸው ህዝቦች በእነዚህ ሁሉ መንገዶች ረክሰዋል፡፡ 25 ምድሪቱ ረከሰች፣ ስለዚህም በኃጢአታቸው ቀጣኋቸው፣ ምድሪቱም በላይዋ የሚኖሩትን ተፋቻቸው፡፡ 26 ስለዚህ እናንተ የእኔን ትዕዛዛትና ህግጋቴን መጠበቅ አለባችሁ፣ እናንተ ተወላጅ እስራኤላዊያንም ሆናችሁ በእንተ መሀል የሚኖሩ እንግዶች ከእነዚህ ያልተገቡ ነገሮች የትኞቹንም ማድረግ የለባችሁም፡፡ 27 ከእናንተ አስቀድሞ በዚህ ምድር የኖሩ ሰዎች የሰሩት ጸያፍነት ይህ ነው፣ እናም አሁን ምድሪቱ ረከሰች፡፡ 28 ስለዚህም ምድሪቱ ከእናንተ በፊት የነበሩትን ሰዎች እንደተፋች እናንተንም ካረከሳችኋት በኋላ እንዳትተፋችሁ ተጠንቀቁ፡፡ 29 ከእነዚህ አስነዋሪ ነገሮች መሀል የትኛውንም ነገር ያደረገ፣ እንዲህ ያለ ነገሮችን ያደረገው ሰው ከህዝቡ መሀል ተለይቶ ይጠፋል፡፡ 30 ስለዚህ በእነዚህ ነገሮች እንዳታረክሱ ከእናንተ አስቀድሞ በዚህ ስፍራ ይፈፀሙ የነበሩትን ጸያፍ ልምዶች ባለማድረግ ትዕዛዛቴን መጠበቅ አለባችሁ፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ።



Leviticus 18:4

ሕጌን ያዘዙ ሥርዐቴንም በጥንቃቄ ጠብቁ

እነዚህ ሁለቱ ሐረጐች በመሠረቱ አንድ ትርጉም ያላቸውና ሕዝቡ እግዚአብሔር ያዘዛቸውን ሁሉ ማድረግ እንዳለበቸው የሚያተኩሩ ናቸው:: ይህን ተጓዳኝ ንጽጽር የእግዚአብሔርን ሕጐች ሁሉ መጠበቅ እንደሚገባቸው እንደ አንድ ዐረፍተ ነገር መተርጐም ይችላሉ አት ሕጐቼንና ሥርዓቶቼን ሁሉ ታዘዙ:: (ተጓዳኝ ንጽጽር ይመልከቱ)

በእነርሱም ኑሩ

የእግዚአብሔርን ሕጐች መታዘዝ አንድ ሰው የሚራመድበት ጐዳና ተደርገው ተነግረዋል:: አት: “ስለዚህ ባሕሪያችሁን በእነርሱ መሠረት ተለማመዱ” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 18:6

ከአባትህ ሚስት ጋር

አንዳንዴ አንድ ወንድ ከአንድ በላይ ሚስቶች ይኖሩታል:: አባቱን ካገባች ከማንኛዋም ሴት ጋር ግብረ ሥጋ ግንኙት ማድረግን እግዚአብሔር አልፈቀደም::

Leviticus 18:9

ከአባትህ ወይም ከእናትህ ሴት ልጅ ጋር

ይህም አንድ ሰው ከተመሳሳይ ወላጅ ወይም የተለየ አባት ወይም እናት ቢኖራትም ከእህቱ ጋር በግብረ ሥጋ አይገናኝ ማለት ነው

በቤት ያደገች ወይም በውጭ የተወለደች ቢትሆን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “በቤት ውስጥ ያደገች ወይም ከቤት ውጭ ያለች ቢትሆን” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የአባትህ ሚስት ለአባትህ ከወለደቻት ሴት ልጅ ጋር ግብረ ሥጋ አትፈጽም

አማራጭ ትርጉሞች እነሆ ፤ (1)ከግማሽ እህትህ ጋር ግብረ ሥጋ አትፈጽም ፤(2)የእንጀራ እህት ጋር እዚህ ያ ሰው ተመሣሣይ አባት ወይ እናት ከሌላት እኀቱ ጋር ማለት ነው፤ወላጆቻቸው በተጋቡ ጊዜ ወንድምና እኀት ሆነዋልና፤

Leviticus 18:12

ለዚያ ዓላማ ወደ እርስዋ አትቅረብ

“የግብረ ሥጋ ግንኙነት ለመፈጸም ወደ እርስዋ አትሂድ”

Leviticus 18:15

ከእርስዋ ጋር አትተኛ

እግዚአብሔር ደጋግሞ የሚናገረው ለትዕዛዙ አጽንዖት ለመስጠት ነው::

Leviticus 18:19

የወር አበባ

ይህ ከሴት ማዕጸን በወራዊ ጊዜ ደም የሚፈስስበት ነው

የባልንጀራህን ሚስት

የማንኛውንም ሰው ሚስት

Leviticus 18:22

ይህ አስጸያፊ ነው

እዚህ “አስጸያፊ” እግዚአብሔር እንዲሆኑ ያደረገውን የተፈጥሮአዊ ነገሮች ሥርዓት መተላለፍን ያመለክታል::

Leviticus 18:24

አሕዛብ…ሁሉ ረክሰዋልና

ይህ በከነዓን የሚኖሩ ሰዎች ያመለክታል:: “ሕዝብ” ወይም “አሕዛብ” የተባለው ሀሳብ “ሰዎች” በሚለው ግልጽ እንደሚሆን አድርገው ይተርጉሙ:: አት የአሕዛብ ሰዎች በእነዚህ ረክሰዋል:: (Metonymy/ምትክ አቻ ትርጉም ያላቸውን ተመሳሳይ አባባሎችን ይመልከቱ)

ምድሪቱም … ረከሰች

“ሰዎች ምድሪቱን አርክሶአታል”

ምድሪቱ…የሚኖሩባትን ሰዎች ተፋቻቸው

እግዚአብሔር ሕዝቡን ከምድሪቱ በጉልበት ማስወጣቱ ምድሪቱ እንደሰው ሰዎችን እንደተፋች ተደርጐ ተነግሮእል (ዘይቤያዊ አነጋገርና በሰውኛ አገላለጽ ይመልኩቱ)

Leviticus 18:26

ከእነኚህ የተጠሉ ድርጊቶች

“ከእነኚህ አስጸያፊ ድርጊቶች”

ይህ ርኩሰት ነው

ይህ “እነዚህን ጸያፍ ድርጊቶች” ያመለክታል

ስለዚህ ተጠንቀቁ

“ስለዚህ እኔን ለመታዘዝ ተጠንቀቁ”

በፊት የነበረውን ሕዝብ እንደተፋች እናንተን እንደትተፋችሁ

እግዚአብሔር ሕዝቡን ከምድሪቱ በጉልበት ማስወጣቱ ምድሪቱ እንደሰው ሰዎችን እንደተፋች ተደርጐ ተነግሮእል:: በዘሌዋዊያን 18:25 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት: “ከዚህም የተነሣ እነርሱን ከምድሪቱ በጉልበት እንዳወጣሁት እናንተንም ከምድሪቱ አወጣለሁ”(ዘይቤያዊ አነጋገርና በሰውኛ አገላለጽ ይመልኩቱ)

Leviticus 18:29

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩ ያበቃል

ሰዎች…ከሕዝቡ ተለይተው ይጥፉ

ከማኀበረሰቡ መገለሉ ሰዎች አንድ ቢጣሽ ጨርቅ ከልብስ ወይም ቅርንጫፍ ከዛፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ እንደተቆረጠ ተደርጐ ተነግሮአል:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እነዚህ ሰዎች በሕዝቡ ዘንድ እንዳይኖሩ ወይም እነዚህን ሰዎች ከሕዝቡ እንዲትለዩአቸው” (ዘይቤያዊ አገላለጽና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ከእናንተ በፊት ካደረጓቸው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ከአናንተ በፊት የነበሩ ሰዎች ያደረጉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በእነዚህ

እዚህ “እነዚህ” ጸያፍ ልምዶችን ያመለክታል::


Chapter 19

1 ሙሴን እንዲህ አለው 2 “ለእስራኤል ሰዎች ጉባኤ ሁሉ እንዲህ ብለህ ንገራቸው፣ “እኔ ያህዌ አምላካችሁ ቅዱስ እንደሆንኩ እናተም ቅዱሳን ሁኑ፡፡ 3 እያንዳንዱ እናቱንና አባቱን ያክብር፣ እናንተም ሰንበቴን ጠብቁ፡፡ እኔ አምላካች ያህዌ ነኝ፡፡ 4 ጥቅም ወደሌላቸው ጣኦታት ዘወር አትበሉ፣ ከቀለጠ ብረት ለራሳችሁ አማልዕክትን አታብጁ፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 5 ለያህዌ የህብረት መስዋእቶችን ስታቀርቡ፣ ተቀባይነት ልታገኙ በምትችሉበት መንገድ አቅርቡ፡፡ 6 መስዋዕቱ ባቀረባችሁበት ቀን አሊያም በማግስቱ ይበላ፡፡ አንዳች ነገር እስ ሶተኛው ቀን ቢተርፍመ ይቃጠል፡፡ 7 በሶስተኛው ቀን ቢበላ የረከሰ ነው፡፡ ተቀባይነት አያገኝም፣ 8 ነገር ግን የበላው ሁሉ በበደለኛነቱ ይጠየቅበታል ምክንያቱም ለያህዌ የተለየውን አርክሷል፡፡ ያ ሰው ከህዝቡ ተለይቶ ይጥፋ፡፡ 9 የምድራችሁን ሰብል በምትሰበስቡበት ጊዜ፤ የእርሻችሁን ቀርጢያ ሁሉ አትልቀሙ፣ አሊያም የአዝመራችን ምርት ሁሉ አትሰብስቡ፡፡ 10 ከወይን ተክልህ እያንዳንዱን ወይን ፍሬ አትሰብስብ፣ አሊያም በወይን ስፍራ የወዳደቁትን የወይን ፍሬዎች አትልቀም፡፡ ለድሆችና ለመጻተኞች እነዚህን ተዉላቸው፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 11 አትስረቁ፡፡ አትዋሹ፡፡ አንዳችሁ ሌላችሁን አታታሉ፡፡ 12 በሃሰት በስሜ አትማሉ የአምላካችን ስም አታርክሱ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 13 ጎረቤትህን አትበድል ወይም አትዝረፈው፡፡ የቀን ሰራተኛውን ክፍያ በአንተ ዘንድ አታሳድር፡፡ 14 መስማት የተሳነውን ሰው አትርገመው ወይም ከእውሩ ፊት ማሰናከያ ድንጋይ አታስቀምጥ ይልቁንም አምላክህን ፍራ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 15 ፍትህን አታጣም፡፡ አንድ ሰው ድሃ ስለሆነ ልታደላለት አይገባም፣ እንደዚሁም አንድ ሰው ባለጸጋ ስለሆነ አታዳላለት፡፡ ይልቁንም ለጎረቤትህ በጽድቅ ፍረድ 16በሰዎች መሃል በሀሳት ሃሜትን አታሰራጭ 16 በሰዎች መሃል ሀሜትን እያሰራጨህ አትዙር፣ ይልቁንም የጎረቤትህን ሕይወት አቅና፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 17 በልብህ ወንድምህን አትጥላ፡፡ በእርሱ ምክንያት የኃጢአቱ ተካፋይ እንዳትሆን ጎረቤትህን በቅንነት ገስጸው፡፡ 18 ከህዝብህ ማንንም አትቀበል ወይም በማንም ላይ ቂም አይኑርህ፣ ነገር ግን በዚህ ፈንታ ጎረቤትህን እንደራስህ ውደድ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 19 ትዕዛዛቴን መጠበቅ አለብህ፡፡ እንስሳትህን ከሌሎች ልዩ ዝርያ ካላቸው እንስሳት ጋር አታዳቅል፡፡ በእርሻህ ላይ ስትዘራ የተለያየ የዘር ዐይነቶችን አትደባልቅ፡፡ ከሁለት የተለያዩ አይነት ነገሮች ተደባልቆ የተሰራ ልብስ አትልበስ፡፡ 20 ቤዛ ካልተከፈለላት ወይም ነጻ ካልወጣች ለባል ከታጨት ባሪያ ከሆነች ልጃገረድ የተኛ ሁሉ ይቀጡ፡፡ ሊገደሉ ግን አይገባም ምክንያቱም ነጻ አልወጣችም፡፡ 21 ሰውዬው ወደ መገናኛው ድንኳን መግቢያ ለበደል መስዋዕት ለያህዌ አውራ በግ ያምጣ፡፡ 22 ከዚያ ካህኑ በያህዌ ፊት ሰውዬው ለሰራው ኃጢአት የበደል መስዋዕት አውራ በግ በማቅረብ ያስተሰርይለታል፡፡ ከዚያ የሠራው ኃጢአት ይቅር ይባልለታል፡፡ 23 ወደምድሪቱ ስትገቡና ለምግብ የሚሆን ሁሉንም ዐይነት ዛፎች ስትተክሉ፣ ዛፎቹ ያፈሩትን ፍሬ ለመብላት እንደተከለከለ ቁጠሩት፡፡ ፍሬው ለእናንተ ለሶስት ዓመታት የተከለከለ ነው፡፡ አይበላም፡፡ 24 ነገር ግን በአራተኛው አመት ፍሬው ሁሉ ለያህዌ ለምስጋና የሚሰዋ ቅዱስ ይሆናል፡፡ 25 አመት ፍሬውን መብላት ትችላላችሁ፡፡ በመጠበቃችሁ ዛፎቹ ብዙ ያፈራሉ፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 26 ደሙ በውስጡ ያለበትን ስጋ አትብሉ፡፡ ስለ ወደፊቱ መናፍስትን አታማክሩ፣ ደግም ከተፈጥሮ በላይ በሆኑ ኃይላት ሌሎችን ለመቆጣጠር አትፈልጉ፤፡፡ 27 እንደ ጣኦት አምላኪዎች የጸጉራችሁን ዙሪያ አትላጩ ወይም የጺማችሁን ዙሪያ አትቆረጡ፡፡ 28 ለሙታን ሰውነታችሁን በስለት አትቁረጡ ወይም በሰውነታችሁ ላይ ንቅሳት አታድርጉ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 29 ሴት ልጅህን ሴተኛ አዳሪ በማድረግ አታወርዳት፣ በዚህ ነገር አገረ ወደ ግልሙትና ትገባለች ምድሪቱም በእርኩሰት ትሞላለች፡፡ 30 ጠብቁ የቤተመቅደሴን ቅድስና አክብሩ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 31 ወደ ሙታን ጠሪዎችና መናፍስትን ወደሚያነጋግሩ ዘወር አትበሉ፡፡ እነዚህን አትፈልጉ፣ ካልሆነ ያረክሷችኋል፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 32 ፀጉሩ ለሸበተ ሰው ተነስለት ደግሞም በዕድሜ የገፋውን ሰው አክብር፡፡ አምላክህን ፍራ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 33 በምድርህ በመካከልህ መጻተኛ ቢኖር፣ አትግፋው፡፡ 34 በመካከላችሁ የሚኖረው መጻተኛ እንደ ተወላጅ እስራኤላዊ ወገናችሁ ቁጠሩት ደግሞም እንደ ራሳችሁ ውደዱት፣ ምክንያቱም እናንተም በግብጽ ምድር መጻተኞች ነበራችሁ፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 35 ርዝመትን፣ ክብደትን፣ ወይም ብዛትን ስትለኩ፡፡ ሀሰተኛ መለኪያ አትጠቀሙ፡፡ 36 ትክክለኛ መስፈሪያን፣ ትክክለኛ ሚዛኖችን፣ ትክክለኛ የኢፍ እና የኢን መለኪያዎችን ተጠቀሙ፡፡ ከግብጽ ምድር ያወጣኋችሁ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 37 ትዕዛዛቴንና ህግጋቴን ሁሉ ጠብቁ፣ አድርጓቸውም፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡”



Leviticus 19:1

ሰንበታቴን ጠብቁ

“ሰንበታቴን አክብሩ” ወይም “ለአረፍኩት ቀን ክብር ስጡ”

ጥቅም ወደሌላቸው ጣዖታት ዘወር አትበሉ

ጣዖታትን ማምለክ ወደ እነሱ ዘወር እንደማለት ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “የማይረቡ ጣዖታትን ማምለክ አትጀምሩ” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 19:5

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገር ይቀጥላል

ተቀባይነት እንዲያገኝላችሁ አድርጋችሁ አቅርቡ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: ሁኔኛ ትርጉሞች እነሆ 1)እግዚአብሔር መስዋዕቱን የሚያቀርበውን ሰው ይቀበላል አት፤ “ እንዲቀበልህ በሥርዓት መሥዋዕትህን አቅርብ” ወይም 2) እግዚአብሔር የሚያቀርበውን ሰው መሥዋዕት ይቀበላል አት፤ “ መስዋዕትህን እንዲቀበል በሥርዓት አቅርብ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ እናም ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ይበላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ይብሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ይቃጠል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ያቃጥሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ቢበላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ቢበሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ተቀባይነት የለውም

የተመደበውን ጊዜ አሳልፎ የቀረበውን መሥዋዕት መብላት መስዋዕቱ የማሸፍነውን በደል መጨመርና እግዚአብሔርን መበደል ነው ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ለመብላት አይቀበሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እያንዳንዱ…የራሱን በደል ይሸከማል

የሰውየው በደል አንድን ግዑዝ ዕቃ ሰው እንደተሸከመ ተደርጐ ተነግሮአል:: እዚህ “በደል” የሚለው ቃል ለዚያ በደሉ የሚሰጠውን ቅጣት ያመለክታል:: አት: ማንኛውም ለራሱ በደል ተጠያቂ ነው ወይም እግዚአብሔር ማንንም ስለኃጢአቱ ይቀጣል:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ወይም ተመሳሳይ ትርጉም ያለቸው ምትክ አባባሎች ይመልከቱ)

ያ ሰው ከሕዝቡ ዘንድ ይወገድ

ሰውየው ከማኀበረሰቡ ዘንድ መገለሉ አንድ ቢጣሽ ጨርቅ ከልብስ ወይም ቅርንጫፍ ከዛፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ እንደተቆረጠ ተደርጐ ተነግሮአል:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: በዘሌዋዊያን 7:2ዐ ይህን አንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት፤ “ሰውየው በሕዝቡ ዘንድ አይኑር ወይም ይህንን ሰው ከሕዝቡ ይለዩት” (ዘይቤያዊ አገላለጽና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 19:9

የምድራችሁን መከር በምትሰበስቡበት ጊዜ በእርሻችሁ ዳርና ዳር ያለውን አትጨዱ

“እህሎቻችሁን በምትሰበስቡበት ጊዜ በእርሻችሁ ዳርና ዳር ያለውን ሙሉውን አትጨዱ”

ቃርሚያውንም አትልቀሙ

ይህ ሁለተኛ ጊዜ ወደኋላ በመመለስ ለመጀመሪያ ጊዜ ሳይሰበሰብ የቀረውን እንደገና መስብሰብን ያመለክታል:: የዚህ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት:: ወደኋላ ተመልሰው የቀረውን ሁሉ አይልቀሙ:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 19:11

በስሜ በሐሰት አትማሉ

“እውነት ላልሆነው ነገር ስሜን በመጠቀም አትማሉ”

Leviticus 19:13

ባልጀራህን አቃጭበርብር ወይም አትቀማውም

እዚህ “ባልጀራ” “ማንኛውም ሰው” ማለት ነው ይህ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት “ባልጀራህን አትጉዳ ወይም አትቀማውም” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የሙያተኛውን ደመወዝ ሳትከፍል አታሳድር

ሥራው በቀኑ በተፈጸመ ጊዜ አስሠሪው ለሠራተኛው ወዲያው መክፈል እንዳለበት እግዚአብሔር ያዝዛል የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉሙ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 19:15

በፍርድ ለማዛባት ምክንያት አትሁኑ

ድርብ አሉታዊ ቃላት ለአትኩሮት ተጠቅመዋል:: ይህ በአዎንታዊ መንገድ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ሁልጊዜ ትክክለኛውን ፍርድ ይስጡ” (See Litotes/ በአሉታዊነት አዎንታዊነትን የመግለጽ አነጋገር ዘይቤ ይመልከቱ)

ለድሃ አታድላ ለባለጠጋ ልዩ አክብሮት አትስጥ

“ድሃ” እና “ባለጠጋ” የተባሉ ቃላት ሁለት ጫፍ የረገጡ አባባሎች ናቸውና ሲጣመሩ “ማንኛውም ሰው” የሚል ትርጉም ይሰጣሉ አነዚህን ጽንሰ ሀሳቦች ግልጽ ለማድረግ ይተርጉሙ:: አት: “ያለውን ገንዘብ ተመልክተህ ለማንኛውም ሰው አታድላ”:: (See Merism/ብዙውን በነጠላ መልቅ የመግለጽ አነጋገር ዘይቤ ይመልከቱ)

ለባልንጀራህ በትክክል ፍረድ

“ለማንኛውም ሰው በትክክለኛነት ፍረድ”

ሐሜት አታንዛ

“ስለሌሎች ሰዎች የሚጐዳውን እውነት ያልሆነውን መልእክቶች አታውራ”

Leviticus 19:17

ወንድምህን በልብህ አትጥላው

አንድን ሰው በቀጣይነት መጥላት ይህን ሰው ከልብ እንደመጥላት ተደርጐ ተነግሮአል:: አት: “ወንድምህን በቀጣይነት አትጥላው” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ባልንጀራህን በግልጽ ገሥጸው

“ኃጢአትን የሚሠራውን ሰው አርመው”

Leviticus 19:19

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

ከሁለት ዓይነት ነገር የተሠራ ልብስ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አንድ ሰው ከሁለት ዓይነት ነገሮች የሠራው ልብስ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 19:20

ለሌላ ከታጨች ሴት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሌላ ሰው ለማግባት ከተስማማች ሴት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ነገር ግን ያልተዋጀች ወይም ነጻ ያልወጣች ብትሆን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ነገር ግን የወደፊት ባልዋ ያልዋጃትና ነጻነት ያልሰጣት ብትሆን” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ይቀጣሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሴት ባሪያዋንና ከእርስዋ ጋር ያመነዘረውን ትቀጣላቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አይገደሉም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አትግደሉአቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ሰውየው የበደሉን መሥዋዕት ወደ እግዚአብሔር ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ ያመጣል፡ ለበደል መሥዋዕት አውራ በግ ያመጣል

“ሰውየውም ለበደል መሥዋዕት የሚሆን አንድ አውራ በግ ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ ለእግዚአብሔር ያምጣ”

ኃጢአቱም ይቅር ይባልለታል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የሠራውን ኃጢአት እግዚአብሔር ይቅር ይልለታል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 19:23

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

ከዚያም ፍሬው ለመብላት የተከለከለ መሆኑን እወቁ ለሶስት ዓመታትም የተከለከለ በመሆኑ አይበላ

እግዚአብሔር መከልከሉን ለማተኮር ደግሞ ይናገራል እናም ለመጀመሪያ ሶስት ዓመታት ፍሬ የሚሰጠውን ዛፍ ይገልጻል አት: “ከዚያም ለመጀመሪያ ሶስት ዓመታት የዛፎች ፍሬ አትብሉ” (ተዛማጅ ንጽጽር ይመልከቱ)

ከዚያም ፍሬው ለመብላት የተከለከለ መሆኑን እወቁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እነርሱ የሚያፈሩትን ፍሬ እንዳትበሉ እኔ ከልክያችኋለሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ፍሬው ተከልክሎአችኋል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ፍሬውን ከልክያችኋለሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አይበላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አትብሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 19:29

ሕዝብ በግልሙትና ምድሪቱ በርኩሰት እንዳትሞላ

እዚህ “ሕዝብ” እና “ምድር” የተባሉ ቃላት በዚያ የሚኖሩ ሰዎችን ያመለክታሉ:: አት፤ “ግልሙትናን ወይም ሌሎች ርኩሰቶችን የሚለማመዱ ሰዎች በዚያ ነገር እንደወደቁ ወይም እንደተሞሉ ተደርገው ተገልጸዋል” አት ሰዎች ግልሙትናንና ርኩስ ተግባራትን መለማመድ ጀመሩ( ተመሳሳይ ምትክ አባባሎችንና ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 19:31

ሙታን ወይም መናፍስት

ሁነኛ ትርጉሞች 1) ሙታንና መናፍስ የተለያዩ ናቸው 2) ይህ ድርብ ቃል ነው የሙታን መናፍስት (See Doublet/ ድርብ ቃላትንና አባባሎችን ይመልከቱ

አትፈልጉአቸው ወይም ያረክሱአችኋል

እንዚያን ሰዎች አትፈልጉአቸው፤ እንደዚያ ካደረጋችሁ ያረክሱአችኋል፡፡

Leviticus 19:32

ተነሥለት

በአንድ ሰውፊት መነሣት የማክበር ምልክት ነው ምልክታዊ ድርጊት ይመልከቱ::

ሽበታሙ ሰው

ከዕድሜ የተነሣ ጸጉሩ የሸበተውን ሰው ወይም ሽማግሌ ሰው ያመለክታል

Leviticus 19:35

ውሸተኛ መሥፈሪያ አትጠቀሙ

ይህ ነገሮች በሚትመዝኑበት ጊዜ በማወቅ ትክክለኛ ልከት የማይሰጡ መሣሪያዎችን የመጠቀም ልምምድን ይከለክላል::

ኢፍ

የእህል መለኪያ ነው (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች ይመልከቱ)

ኢን

የፈሳሽ መለኪያ ነው (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች ይመልከቱ)


Chapter 20

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‹ከእስራኤል ሰዎች መሃል ማንም ሰው፣ ወይም ማንኛውም በእስራኤል የሚኖር መጻተኛ ከልጆቹ መሃል አንዱን ለሞሎክ ቢሰጥ በዕርግጥ ይገደል፡፡ በምድሪቱ የሚኖሩ ሰዎች በድንጋይ ይውገሩት፡፡ 3 እኔም በዚያ ሰው ላይ ፊቴን አዞርበታለሁ፣ ከህዝቡም መሃል እቆርጠዋለሁ ምክንያቱም የተቀደሰውን ስፍራዬን ለማርከስና ቅዱሱን ስሜን ለማቃለል ልጁን ለሞሎክ ሰጥቷል፡፡ 4 ያ ሰው ከልጆቹ አንዱን ለሞሎክ ሲሰጥ ዚያች ምድር ሰዎች እንዳላዩ ቢሆን፣ ባይገድሉት፣ 5 እኔ ራሴ በዚያ ሰውና በቤቱ ላይ ፊቴን አዞራለሁ፣ እኔ ቆርጬ እጥለዋለሁ እንደዚሁም ከሞሎክ ጋር በሚያመነዝረው በማንኛውም ላይ ይህን አደርጋለሁ፡፡ 6 ወደ ሙታን ጠሪዎች ዘወር የሚል፣ ወይም ከመናፍስት ጋር ከሚነጋገሩ ጋር የሚመነዝርን ሰው ፊቴን አዞርበታለሁ፤ ከህዝቡም መሃል አጠፋዋለሁ፡፡ 7 ስለዚህ ራሳችሁን ለያህዌ ስጡ ተቀደሱም፣ ምክንያቱም እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 8 ትዕዛዛቴን ጠብቁ አድርጓቸውም፡፡ ለራሴ የመረጥኳችሁ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 9 ወይም እናቱን የሚረግም ሁሉ ይገደል፡፡ አባቱን ወይም እናቱን ረግሟልና በደለኛ ነው ሞት ይገባዋል፡፡ 10 ከሌላ ሰው ሚስት ጋር ዝሙት የፈጸመ ሰው፣ ከጎረቤቱ ሚስት፣ ጋር ያመነዘረ ይገደል አመንዝራውና አመንዝራይቱም ሁለቱም ይገደሉ፡፡ 11 ከአባቱ ሚስት ጋር ሊተኛት የወደቀ የገባ አባቱን ያዋርዳል፡፡ ልጅየውም የአባቱ ሚስትም ሁለቱም ይገደሉ፡፡ በደለኞች ናቸው ሞት ይገባቸዋል፡፡ 12 አንድ ሰው ከልጁ ሚስት ጋር ቢተኛ፣ ሁለቱም ሊገደሉ ይገባል ያልገባ ፍትወት ፈጽመዋል በደለኞች ናቸው ሞት ይገባቸዋል፡፡ 13 አንድ ወንድ ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከሌላ ወንድ ጋር ቢተኛ፣ ሁለቱም ጸያፍ ነገር አድርገዋል፡፡ በእርግጥ ሞት ይገባቸዋል፡፡ ይገደሉ፡፡ በደለኞች ናቸው ሞት ይገባቸዋል፡፡ 14 አንድ ሰው አንዲትን ሴትና እናቲቱንም ቢያገባ፣ ይህ አሳፋሪ ነው፡፡ እርሱና ሴቲቱ ሁለቱም በእሳት ይቃጠሉ፣ ይህ ሲደረግ በመሀላችሁ ክፋት አይኖርም፡፡ 15 አንድ ሰው ከእንስሳ ጋር ቢተኛ፣ በእርግጥ ይገደል፣ እንስሳይቱንም ግደሏት፡፡ 16 አንዲት ሴት ለመገናኘት ወደ ማንኛውም አይነት እንስሳ ብተቀርብ ሴትየዋንም እንስሳውንም ግደሏቸው፡፡ በእርግጥ ሊገደሉ ይገባል፡፡ በደለኞች ናቸው ሞት ይገባቸዋል፡፡ 17 አንድ ሰው የአባቱ ልጅ ከሆነችውም ሆነ የእናቱ ልጅ ከሆነች እህቱ ጋር ቢተገኛ እህትም ከእርሱ ጋር ብትተኛ ይህ አሳፋሪ ነገር ነው፡፡ ከህዝባቸው መሃል ተለይተው ይውጡ፤ ምክንያቱም ከእህቱ ጋር ተኝቷል፡፡ በደሉን ይሸከማል፡፡ 18 አንድ ሰው አንዲትን ሴት በወር አበባዋ ወቅት አብሯት ቢተኛና ቢገናኛት፣ የደሟ ምንጭ የሆነውን የደም መፍሰሷን ገልጧል፡፡ ወንዱም ሴቷም ሁለቱም ከህዝባቸው መሃል ተለይተው ይውጡ፡፡ 19 ከእናትህ ወይም ከአባትህ እህት ጋር አትተኛ፣ ምከንያቱም የቅርብ ቤተ ዘመድህን ታዋርዳለህ፡፡ በደልህን ልትሸከም ይገባሃል፡፡ 20 አንድ ሰው ከአጎቱ ሚስት ጋር ቢተኛ አጎቱን አዋርዷል፡፡ በደላቸውን ሊሸከሙ ይገባል ያለ ልጅ ይቀራሉ፡፡ 21 አንድ ሰው የወንድሙን ሚስት ቢያገባ ይህ እርኩስ ነው ምክንያቱም ዘመዱ ሆኖ ሳለ የወንድሙን ትዳር አፍርሷል፣ ልጅ አልባ ይሆናሉ፡፡ 22 ስለዚህም ስርአቶቼንና ህግጋቶቼን ሁሉ መጠበቅ አለባችሁ፤ እንድትኖርባት ያመጣኋቸው ምድር እንዳትተፋችሁ ህግጋቴንና ሥርዓቶቼን ጠብቁ፡፡ 23 ከፊታችሁ በማባርራቸው ህዝቦች ልምዶች አትመላለሱ፣ እነርሱ እነዚህን ነገሮች ሁሉ አድርገዋል፣ እኔም እነርሱን ጠላሁ፡፡ 24 እኔ እንዲህ እላችኋለሁ፣ “ምድራቸውን ትወርሳላችሁ፣ ምድሪቱን እንድትወርሷት ለእናንተ እሰጣችኋለሁ፣ ወተትና ማር የምታፈስ ምድር ናት፡፡ ከሌላው ህዝብ የለየኋችሁ፣ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ” 25 ስለዚህ እናንተ ንጹህ በሆኑና ንጹኅ በሆኑ እንስሳት መሃል፣ ንጹኅ በሆኑና ንጹህ ባልሆኑ ወፎች መሃል ልዩነት አድርጉ፡፡ ለእናንተ ርኩስ ናቸው ብዬ በለየኋቸው ንጹኅ ባልሆኑ እንስሳት ወይም ወፎች ወይም በማንኛውም በምድር ላይ በሚሳብ ፍጥረት ራሳችሁን አታርክሱ፡፡ 26 እኔ ያህዌ ቅዱስ እንደሆንኩ፣ ደግሞም ለእኔ ትሆኑ ዘንድ ከሌሎች ህዝቦች እንደለየኋችሁ ቅዱሳን ሁኑ፡፡ 27 ከሙታን ጋር የሚነጋገር አንድ ወንድ ወይም አንዲት ሴት ወይም ከመናፍስት ጋር የሚነጋገር በእርግጥ ይገደል፡፡ ህዝቡ በድንጋይ ወግፎ ይግደላቸው በደለኞች ናቸውና ሞት ይገባቸዋል፡፡



Leviticus 20:1

ከልጆቹ አንዱን ለሞሎክ የሚሰጥ

ሞሎክን የሚያመልኩ ልጆቻቸውን በእሳት መሥዋዕት አድርገው ያቀርባሉ የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት: “ለሞሎክ እንደመስዋዕት ከልጆቹ ማንኛውን የሚገድል” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በእርግጥ ይገደል፤እርሱንም የአገሬው ሰው በድንጋይ ይውገረው፡፡

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የአገረው ሕዝብ በድንጋይ ወግረው ይግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 20:3

እኔ ደግሞ በዚያ ሰው ላይ ጠላት እሆናለሁ

ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር የሚገልጸው “በጥብቅ መወሰኑን” ነው:: አት: “ይህን ሰው ሊጠላው በአእምሮዬ ወስኛለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ፊቴም ጠልቶታል

በቁጣ ተሞልቻለሁ

ልጁን ሰጠ

ልጁን መስዋዕት አደረገ

መቅደሴን አርክሶአልና ቅዱስ ስሜንም አቃልሎአልና

“እናም ይህን በማድረጉ መቅደሴን አርክሶአል ቅዱስ ስሜንም አቃልሎአል”

ቅዱስ ስሜንም አቃልሎአል

የእግዚአብሔር ስም እግዚአብሔርንና ምሥክርነቱን ይገልጻል:: አት: “ምሥክርነቴን አላከበራችሁም” ወይም “አላከበራችሁኝም” (ተመሣሣይ ምትክ አባባሎችና ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አይተው ቸል ቢሉ

አይተው ቸል ቢሉ" የሚለው ሀረግ ማየት እንደተሳናቸው ይገልጻል ይህ የሚናገረው አንድን ነገር እንዳላዩ ቸል ማለትን ነው:: (ተመሳሳይ ምትክ አባባሎች ይመልከቱ)

ከሞሎክ ጋር በማመንዘር እርሱን የሚከተሉትን

ይህ ሀረግ ለእግዚአብሔር ታማኝ ያለሆኑትን ከአመንዝራዎች ጋር ያነጻጽራል:: አት: “ለእግዚአብሔር ታማኝ ያልሆኑት” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 20:6

ከእነርሱም ጋር በሚያመነዝር ሰው

ይህ ሀረግ ታማኝ ያለሆኑ ሰዎችን ከአመንዝራዎች ጋር ያነጻጽራል:: አት: “ይህን በማድረጋቸው ከእኔ ሳይሆን ከመናፍስት ምክርን ይሻሉ” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

በዚያ ሰው ላይ ጠላት እሆንበታለሁ

ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር “በጥብቅ መወሰኑን” ይገልጻል:: አት: ያን ሰው ሊጠላው በአእምሮዬ/በሀሳቤ ወስኛለሁ:: (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ )

ፊቴም ጠልቶታል

በቁጣ ተሞልቻለሁ

Leviticus 20:8

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል

ሥርዓተን ጠብቁ አድርጉትም

“ጠብቁ” “አድርጉ” የሚሉ ቃላት በመሠረቱ አንድ ናቸው:: እነዚህ ቃላት በአንድነት የተቀመጡት ሰዎች እግዚአብሔርን መታዘዝ እንዳለባቸው ትኩረት ለመስጠት ነው:: (Parallelism/ተመሣሣይ ተጓዳኝ ቃላት ይመልከቱ)

በእርግጥ ይገደል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ በእርግጥ ግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 20:10

አንድ ሰው ከባልንጀራው ሚስት ጋር ቢያመነዝር

የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: “ከማንም ሰው ሚስት ጋር የሚያመነዝር ሰው” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በእርግጥ ይገደል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ በእርግጥ ሁለቱንም ግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ከአባቱ ሚስት ጋር የሚተኛ

ይህ አንድ ሰው ከአባቱ ሚስት ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙት ማድረጉን ለዛ ባለ አባባል ይገልጻል:: አንዳንድ አባባሎች እንደ “አባቱ ሚስት ጋር ግብረ ሥጋ ግንኙነት አደረገ” የሚሉ በጣም ቀጥተኛ ሀረጐችን ይጠቀማሉ:: (See Euphmism/ንኣብነት ወይም ለዛ ያለ ወይም በተዘዋዋሪነት አንድን ነገር ስለሚገልጹ ቃላት ይመልከቱ)

ነውር አድርገዋል

እዚህ አንድ ሰው ከልጁ ሚስት ጋር ግብረ ሥጋ ግንኙት መፈጸም እግዚአብሔር ነውር የከፋ ኃጢአት ይለዋል:: በዘሌዋዊያን 18:23 ነውር እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Leviticus 20:13

አንድ ሰው ወንድ ሰው ቢተኛ

ይህ ከሌላ ወንድ ጋር ግብረ ሥጋ ግንኙነት መፈጸሙን ለዛ ባለ አባባል ይገልጻል አንዳንድ አባባሎች እንደ “አንድ ወንድ ሰው ግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጸመ” የሚሉ በጣም ቀጥተኛ ሀረጐችን ይጠቀማሉ:: (See Euphmism/ንኣብነት ወይም ለዛ ያለ ወይም በተዘዋዋሪነት አንድን ነገር ስለሚገልጹ ቃላት ይመልከቱ)

እንዲሁም ከሴት ጋር ቢተኛ

ከወንድ ጋር እንደፈጸመው ከሴት ጋር ቢፈጽም፤ አት: “እንዲሁ ከሴት ጋር ቢፈጽም” (See Simile/ተመሣሣይ አባባሎችን/ድርጊቶችን ይመልከቱ

ጸያፍ ነገር

“አሳፋሪ ነገር” ወይም “የሚዘገንን ነገር”

በእርግጥ ይገደሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ በእርግጥ ግደሉአቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ሰውየውና ሴቶቹ በእሳት ይቃጠሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሰውየውንና ሴቶቹን ሁለቱንም በእሳት ይቃጥላችሁ ግደሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 20:15

በእርግጥ ይገደል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “በእርግጥ ግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ሴቲቱንና እንስሳውን ግደሉ በእርግጥ ይገደሉ

ሁለቱም ሀረጐች ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: እንስሳውና ሴቲቱ እንዲሞቱ አጽንዖት የሰጣሉ:: (Parallelism/ተመሣሣይ ተጓዳኝ አባባሎች ይመልከቱ)

በእርግጥ ይገደሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “በእርግጥ ግደሉአቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 20:17

አንድ ሰው ቢተኛ

ይህ አንድ ሰው ከእህቱ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙት መፈጸሙን ለዛ ባለ አባባል ይገልጻል:: አንዳንድ አባባሎች እንደ “አንድ ሰው ግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጸመ” የሚሉ በጣም ቀጥተኛ ሀረጐችን ይጠቀማሉ:: (See Euphmism/ንኣብነት ወይም ለዛ ያለ ወይም በተዘዋዋሪነት አንድን ነገር ስለሚገልጹ ቃላት ይመልከቱ)

ከአባቱ ሴት ልጅ ወይም ከእናቱ ሴት ልጅ ጋር

ከተለየ አባት ወይም እናት ቢትሆንም ከእህቱ ጋር ግብረሥጋ ግንኙነት መፈጸም አይችልም የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “ሙሉ እህት ወይም ግማሽ እህት ብትሆንም” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ተቆርጦ ይወገድ ወይም ተለይቶ ይጥፋ

ከማኀበረሰቡ የተገለለው ሰው ብጣሽ ጨርቅ ከልብስ ወይም ቅርንጫፍ ከዛፍ እንደሚቆረጥ ከሕዝቡ ተቆርጦ እንደተወገደ ተደረጐ ተገልጾአል ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: ይህን ሃሳብ በዘልዋዊያን 7:2ዐ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ አት፤ “ያ ሰው በሕዝቡ ዘንድ አይኑር” ወይም “ያን ሰው ከሕዝቡ ለዩት” (ዘይቤይዊ አነጋገር ወይም ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በደሉን ይሸከማል

ይህ ሀረግ ሰውየው በኃጢአቱ ይጠየቅበታል ማለት ነው:: አት: “በኃጢአቱ ተጠያቂ ነው” ወይም “ቅጡት” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የወር አበባ ጊዜ

“ለአንድ ሴት በየወሩ ከማዕጸንዋ ደም የሚፈስስባት ጊዜ”

የፈሳሽዋን ምንጭ ገልጦአልና

በወር አበባዋ ጊዜ ከሴት ጋር ግንኙነት ማድረግን አንድ የተደበቀ ነገር ሽፋን መግለጥ ጋር ያነጻጽራል ይህ አሳፋሪ አድራጐት መሆኑ መገለጽ አለበት አት የደምዋን ፍሳሽ በመግለጡ አሳፋሪ ነገር አድርጐአል:: (ዘይቤያዊ አገላለጽ ግምታዊ አውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሰውየውና ሴቲቱ ሁለቱም ተለይተው ይጥፉ

ይህ ለምን መደረግ እንዳበት በግልጽ ይነገር:: ይህን አሳፋሪ ተግባር ስለፈጸሙ ሰውየው ሴቲቱም ሁለቱ ተለይተው ይጥፉ (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 20:19

ቢተኛ

ይህ አንድ ሰው ከአባቱ እኀት ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙት መፈጸሙን ለዛ ባለ አባባል ይገልጻል:: አንዳንድ አባባሎች እንደ “አንድ ሰው ግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጸመ” የሚሉ በጣም ቀጥተኛ ሀረጐችን ይጠቀማሉ:: (See Euphmism/ንኣብነት ወይም ለዛ ያለ ወይም በተዘዋዋሪነት አንድን ነገር ስለሚገልጹ ቃላት ይመልከቱ)

በደላችሁን ትሸከማላችሁ

“በደላችሁን ትሸከማላችሁ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር “በኃጢአታችሁ ትጠየቃላችሁ” ማለት ነው:: አት: “በኃጢአታችሁ ትጠየቁታላችሁ” ወይም “እቀጣችኋለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)::

ከወላጆቻቸው የወረሱትን ማንኛውንም ንብረት ከልጆቻቸው እወስዳለሁ

በብዙዎች የመጽሐፍ ቅዱስ ሕተመቶች ይህ “ያለ ልጅ ይቀራሉ” ተብሎ ተተርጉሞአል::

Leviticus 20:22

እንዲትኖሩባት እናንተን የማስገባባት ምድር እንዳትተፋችሁ

ይህ ሀረግ መጥፎ ምግብን ባለመቀበል እንደሚተፋ ሰው ምድሪቱ እንደምትተፋቸው ይገልጻል ምግብን ካለመቀበል ፈንታ ምድሪቱ ሰዎችን አትቀበልም ታስወጣችኋለች:: በዘለዋዊያን 18 25 ይህን ፈሊጣዊ አባባል እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት “የማስገባባት ምድር እንዳትተፋችሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ሰውኛ አገላለጽ ይመልከቱ)

አትከተሉ

የጣዖት አድራጊዎች ተግባራት መለማመድ የእነርሱን መንገድ እንደመከተል ተደርጐ ተገልጾአል:: አት: “አትከተሉአቸው ዘይቤይዊ አነጋገር’ ይመልከቱ::

አስወጡ

አስወግዱ

Leviticus 20:24

ማርና ወተት የሚታፈሰውን አገር

ማርና ወተት መፍሰስ የሚለው ሀረግ ለሁሉ ሰው በቂ ምግብ የያዘ ባለጸጋና ፍሬያማ ማለት ነው:: አት: “ለእንስሳትና ለእርሻ እጅግ አመቺ አገር” ወይም “ፍሬያማ ምድር “ (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 20:26

ለየኋችሁ

ለይቻችኋለሁ ወይም የራሴ አድጌአችኋለሁ

Leviticus 20:27

ጠሪ

መነጋገር የሚሞክር

በእርግጥ ይገደል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “በእርግጥ ግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)


Chapter 21

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው “ለካህናቱ፣ ለአሮን ልጆች እንዲህ በላቸው፣ ‹ከእናንተ መሃል ማንም በመካከላችሁ በሞተ ሰው አይርከስ፣ 2 ለቅርብ ዘመድ ካልሆነ በስተቀር ማንም አይርከስ ለእናቱ እና አባቱ፣ ለወንድ ልጁና ለሴት ልጁ፣ ወይም ለወንድሙ 3 ወይም በቤቱ ከምትኖር ባል ካላገባች ልጃገረድ እህቱ በስተቀር አይርከስ፡፡ ለእርሷ ግን ራሱን ንጹህ ላያርግ ይችላል፡፡ 4 ለሌሎች ዘመዶቹ ግን እስኪረክስ ድረስ ራሱን ማርከስ የለበትም፡፡ 5 ካህናት ራሳቸውን አይላጩ ወይም የጺማቸውን ዳርቻ አይላጩ፣ አሊያም ሰውነታቸውን በስለት አይቁረጡ፡፡ 6 እነርሱ ለአምላካቸው የተለዩ ይሆኑ፣ የአምላካቸውን ስም አያቃሉ፣ ምክንያቱም ካህናቱ የአምላካቸውን “ምግብ” መስዋዕቱን ለያህዌ በእሳት ያቀርባሉ፡፡ ስለዚህም እነርሱ የተለዩ ይሁኑ፡፡ 7 ለአምላካቸው የተለዩ ስለሆኑ ማናቸውንም ጋለሞታ እና የረከሰች ሴት እንደዚሁም ከባሏ የተፋታችን ሴት ማግባት የለባቸውም፡፡ 8 የአምላክህን “ምግብ” የሚያቀርብ ነውና እርሱን መለየት አለብህ፡፡ በፊትህ ቅዱስ መሆን አለበት፣ ምክንያቱም ለራሴ የለየሁህ እኔ፣ ያህዌ ቅዱስ ነኝ፡፡ 9 ማንኛዋም የማንኛውም ካህን ሴት ልጅ ጋለሞታ ብትሆን አባቷን ታሳፍራለች፡፡ በእሳት ትቃጠል፡፡ 10 ከወንድሞቹ መሃል ሊቀ ካህን የሆነው፣ የሹመቱ ዘይት በራሱ ላይ የፈሰሰበት፣ ደግሞም የሊቀ ካህኑን ልዩ ልብሶች ለመልበስ የተጾመ ጸጉሩን ይሸፍን ልብሱን አይቅደድ፡፡ 11 ለአባቱ ወይም ለእናቱም ቢሆን እንኳን የሞተ ሰው በሚገኝበትና ራሱን በሚያረክስበት ማናቸውም ስፍራ አይሂድ፡፡ 12 ሊቀካህኑ የቤተ መቅደሱን የተቀደሰ ስፍራ ትቶ አይሂድ ወይም የአምላኩን ቅድስና አያቃል፣ ምክንያቱም በአምላኩ የቅባት ዘይት ሊቀ ካህን ሆኖ ተሾሞ ነበርና፡፡እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 13 ካህኑ ድንግሊቱን ሚስቱ አድርጎ ያግባት፡፡ 14 ባሏ የሞተባትን ሴት፣ የተፋታችን ሴት፣ ወይም ጋለሞታን ሴት አያግባ፡፤ እንዲያ ካሉት ሴቶች መሃል አያግባ፡፡ ከራሱ ህዝብ መሃል ድንግሊቱን ብቻ ማግባት ይችላል፡፡ 15 እነዚህን ህጎች ይጠብቅ፣ በህዝቡ መሃል ልጆቹን እንዳያረክስ ህግጋቱን ይጠብቅ፣ እርሱን ለራሴ የለየሁት እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 16 ያህዌ እንደህ ሲል ሙሴን ተናገረው፣ 17 “አሮንን እንዲህ ብለህ ንገረው፣ ማናቸውም ከወገንህ መሀል በትወልዳቸው ውስጥ አካላዊ ጉድለት ያለበት፣ የአምላኩን ‹ምግብ› ለመሰዋት መቅረብ የለበትም፡፡ 18 ማናቸውም አካላዊ እንከን ያለበት ሰው ወደ ያህዌ መቅረብ የለበትም፣ እንደ ዐይነ ስውር፣ ሽባ የሆነ ሰው፣ አካሉ የጎደለ ወይም አካሉ የተወላገደ፣ 19 እጆቹ ወይም እግሮቹ ሽባ የሆነ፣ 20 መጻጉ ወይም ድንክ ሰው፣ ወይም በዐይኖቹ ላይ እንከን ያለበት ሰው፣ ወይም በሽታ የያዘው፣ ሞጭሟጫ፣ እከክ ያለበት ወይም ጃንደረባ ወደ ያህዌ አይቅረብ፡፡ 21 ከካህኑ ከአሮን መሃል ምንም አካላዊ ጉድለት ያለበት ሰው ለያህዌ የእሳት መስዋዕቶች ለመሰዋት አይቅረብ፡፡ አካላዊ ጉድለት ያለበት እንዲህ ያለው ሰው የአምላኩን ‹ምግብ ለማቅረብ መቅረብ የለበትም፡፡ 22 ከቅድስተ ቅዱሳኑም ሆነ ከቅዱሱ የአምላኩ ምግብ ሊበላ ግን ይችል፣ 23 ሆኖም፣ ወደ መጋረጃው መግባት የለበትም ወይም ወደ መሰዊያው አይቅረብ፣ ምክንያቱም አካላዊ ጉድለት ያለበት፣ ስለዚህም ቅዱሱን ስፍራዬን አያርክስ፣ ለራሴ የለየኋቸው እኔ ያህዌ ነኝ፡፡” 24 ሙሴ እነዚህን ቃላት ለአሮን፣ ለልጆቹ፣ እና ለእስራኤል ሰዎች ሁሉ ተናገረ፡፡



Leviticus 21:1

ራሱን ያረክሳል

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባ ሰው ርኩስ ተብሎአል (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በሕዝቡ ወይም በዘመዶቹ መካከል

በእራኤላዊያን መካከል

ድንግል

ያላገባች ወጣት ሴት

Leviticus 21:4

አይላጩ::

ካህናቶች የጢማቸውን ዙሪያ አይላጩ:: እዚህ ጸሐፊው ምን ለማለት እንደፈለገ ግልጽ ላይሆን ይችላል:: ሁኔኛ ትርጉሞች እነሆ 1) የጢማቸውን ከፊሉን ክፍል ይላጩ:: 2) ማንኛውንም የጢም ክፍል አይላጩ::

የተቀደሱ ይሁኑ

የተለዩ ይሁኑ

የአምላካቸውን ስም አያርክሱ

“ስም” የሚለው ቃል የእግዚአብሔርን ባህሪይ ያመለክታል:: አት: “የእግዚአብሔርን ምሥክርነት እታቃልሉ ወይም እግዚአብሔርን አያቃልሉ” (ተመሣሣይ ምትክ አባባሎችን ይመልከቱ)

የአምላካቸውን ምግብ

እዚህ ምግብ አጠቃላይ ምግብን ያመለክታል እግዚአብሔር እነዚህ የሚቀርቡ መሥዋዕቶችን አይመገብም:: እግዚአብሔርን የሚያስደስተውን የምግብ መሥዋዕት የሚያቀርቡ ሰዎች ቅንነትን ነው: (See Synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 21:7

አያግቡ

ካህናት አያግቡ

የተቀደሱ ናቸው

ለተለዩ ናቸው

ቀድሰው

ካህኑን እንደቅዱስ ቁጠሩት

የአምላክህን ምግብ የሚያቀርብ ነውና

እዚህ ምግብ አጠቃላይ ምግብን ያመለክታል እግዚአብሔር እነዚህ የሚቀርቡ መሥዋዕቶችን አይመገብም:: እግዚአብሔር ምግብን እንደማይመገብ ግልጽ በማድረግ ይህን ይተርጉሙ (See Synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ቅዱስ ይሁንላችሁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እንደ ቅዱስ ቁጠሩት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በእሳት ትቃጠል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “በእሳት አቃጥሉአት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 21:10

አጠቃላይ መረጃ

ካህናት ማድረግ ያለባቸው ምን እንደሆነ እግዚአብሔር ለሙሴ በናገሩ ይቀጥላል

የመቀብያ ዘይት

አዲስ ልቀካህን ለይቶ በመቀባት ሥርዓተ በዓል የሚጠቀሙበት የመቀብያ ዘይት ነው:: የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይጠቀሙ

የቅባቱ ዘይት በራሱ ላይ የሆነና የተለየ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “በራሱ ላይ የመቀብያ ዘይት ያፈሰሱበትና የለዩት ሰው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ጸጉሩ አይንጭ ልብሱን አይቅደድ

ራስ መንጨትና ልብስ መቀደድ የሀዘን ምልክቶች ናቸው:: የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 21:13

ከወገኖቹ በካከል

ከራሱ ጐሣ ከሌዊ ጐሣ

ከወገኖቹ መካከል ዘሩን አያርክስ

የረከሰችውን ወይም ያልተገባችውን ሴት በማግባት ካህኑ የሚወልዱአቸው ልጆች ለእርሱ ያልተገቡ ይሆናሉ:: አት: “ያልተገባችውን ሴት በማግባት ያልተገቡ ልጆች አይኑሩት” (ፈሊጣዊ አነጋር ይመልከቱ)::

Leviticus 21:16

የአምላኩን ምግብ የሠዋ ዘንድ አይቅረብ

የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “በእግዚአብሔር መሠዊያ ላይ የሚቃጠለውን የእህል መሥዋዕት ለማቃጠል አይቅረብ” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 21:18

ወደ እግዚአብሔር አይቅረብ

አንድ ካህን ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ ዝርዝር አካላዊ መሥፈርቶችን ማሟላት አለበት:: ይህም የአካል ጐዶሎነት የኃጢአት ወጤት ወይም ማንኛውም የአካል ጐዶሎነት ያለው ሰው ወደ እግዚብሔር መቅረብ አይችልም ማለት አይደለም::

የፊቱ ገጽታ ወይም የሰውነቱ ቅርጽ የተበላሽ

“ፊቱና አካሉ የተበላሸ”

የአምላኩን ምግብ ለማቅረብ

“ምግብ” አጠቃላይ ምግብ ያመለክታል:: አት “በእግዚአብሔር መሠዊያ የሚቃጠል የእህል መሥዋዕት ለማቅረብ” (See Synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ ሙሉን እንደክፍል የመግለጽ ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 21:22

እርሱም

እዚህ “እርሱ” የአካል ጐዶሎነት ያለውን ካህን ያመለክታል

የአምላኩን ምግብ ይብላ

የአምላኩን ምግብ መሥዋዕቶች ይብላ ከመሥዋዕቶቹ ከፊሎች የካህናት ናቸውና ሊበሉ ይችላሉ

የተቀደሰውንና እጅግ ቅዱስ የሆነውን

ይህ ደግሞ መሥዋዕት ሆኖ ስለቀረበው ምግብ ነው የዚህ ዐረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት ከእነዚህ አንዳንድ መሥዋዕቶች በቅዱስ ሥፍራ ቀርበዋል ወይም ከእነዚህ አንዳንዶች በቅዱሳነ ቅዱሳን ቀርበዋል:: (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ለልጆቹ

“ለአሮን ልጆች”


Chapter 22

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 2 “ለአሮንና ለልጆቹ እንዲህ በላቸው፣ የእስራኤል ሕዝብ ለእኔ ከለይዋቸው የተቀደሱ ነገሮች እንዲጠበቁ ንገራቸው፡፡ የተቀደሰው ስሜን አያርክሱ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 3 እንዲህ በላቸው፣ በዘመን ሁሉ ከትውልዳችሁ መሀል ማንም ንጹህ ያልሆነ ሰው የእስራኤል ህዝብ ለያህዌ ወደ ለየው ቅዱስ ነገሮች ቢቀርብ፣ ያ ሰው እኔ ፊት ከመቅረብ የተከለከለ ነወ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 4 ከአሮን ትውልድ ውስጥ ተላላፊ የቆዳ በሽታ ያለበት፣ ወይም ከሰውቱ ፈሳሽ የሚወጣ ንጹኅ እስኪሆን ድረስ ለያህዌ ከሚቀርብ መስዋዕት አይብላ፡፡ማንም ከሞተ ጋር በመነካካት ንጹህ ያልሆነውን ማንኛውንም ነገር የነካ፣ ወይም የዘር ፈሳሽ ካለበት ሰው ጋር በመነካካት፣ 5 ወይም የሚያረክሰውን ማናቸውንም በሆዱ የሚሳብ እንስሳ የነካ፣ ወይም ማናቸውንም የሚያረክሰውን ሰው የነካ፣ ማንኛውም አይነት እርኩሰት የሚያስከትል ነገር የነካ 6 ማናቸውንም እርኩስ ነገር የነካ ካህን እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ ሰውነቱን በውሃ ካልታጠበ በቀር ከተቀደሱት ነገሮች አንዳች አይብላ፡፡ 7 ፀሐይ ስትጠልቅ፣ በዚያን ሰዓት ንጹህ ይሆናል፡፡ ፀሐይ ከጠለቀች በኋላ ከተቀደሱት ነገሮች መብላት ይችላል፣ ምክንያቱም ለእርሱ የተፈቀዱ ምግብ ናቸው፡፡ 8 ሞቶ የተገኘን ማናቸውም ነገር አይብላ ወይም እርሱን የሚያረክሰውን በዱር እንስሳ የተገደለውን አይብላ፡፡ 9 ካህናት ትእዛዛቴን ይጠብቁ፣ ይህን ካላደረጉ በኃጢአት በደለኛ ይሆናሉ ደግም ስሜን በማቃለል ይሞታሉ፡፡ ለራሴ የለየኋቸው እኔ ያህዌ ነኝ፣ 10 ማንም የካህኑ ቤተሰብ ያልሆነ ሰው፣ የካህኑን እንግዶች ጨምሮ፣ ወይም ቅጥር አገልጋዮቹ ጭምር ቅዱስ ከሆነው አንዳች አይብሉ፡፡ 11 ነገር ግን ካህኑ በገንዘቡ ባሪያ ቢገዛ ያ ባሪያ ለያህዌ ከተለዩ ነገሮች መብላት ይችላል፡፡ የካህኑ ቤተሰብ አባላት እና በቤቱ የተወለዱ ባሪያዎች ከእርሱ ጋር ከእነዚህ የተቀደሱ ነገሮች መብላት ይችላሉ፡፡ 12 የካህኑ ሴት ልጅ ካህን ያልሆነ ሰው ብታገባ ለመስዋዕት ከመጣው ውስጥ አንዳች አትበላም፡፡ 13 ነገር ግን የካህኑ ሴት ልጅ ባሏ የሞተባት ከሆነች፣ ወይም ከባሏ ከተፋታች፣ እና ልጅ ያልወለደች ከሆነች እንደ ልጅነቷ ዘመን ለመኖር ወደ አባቷ ቤት ብትመለስ ከአባቷ ምግብ መብላት ትችላለች፡፡ ነገር ግን ማንም የካህን ቤተሰብ ያልሆነ ከካህናት ምግብ መብላት አይችልም፡፡ 14 አንድ ሰው ሳያውቅ ቅዱሱን ምግብ ቢበላ፣ ከወሰደው አንድ አምስተኛ ጨምሮ ለካህኑ ይመልስ፡፡ 15 የእስራኤል ህዝብ ለያህዌ የወዘወዙትንና ያቀረቡትን ቅዱስ ነገሮች ማቃለል የለባቸውም፣ 16 ያልተፈቀደላቸውን ቅዱሱን ምግብ በመብላት ራሳቸውን በደለኛ የሚያደርጋቸውን ኃጢአት እንዲሸከሙ ማድረግ የለባቸውም እነርሱን ለራሴ የለየሁት እኔ ያህዌ ነኝ” 17 ያህዌ እንዲህ አለው፣ 18 “ለአሮንና ልጆቹ እንዲሁም ለእስራኤል ሰዎች ሁሉ እንዲህ በላቸው፣ ‹ማንኛውም እስራኤላዊ፣ ወይም በእስራኤል የሚኖር ባይተዋር፣ ለስዕለትም ይሁን፣ ወይም ለበጎ ፈቃድ መስዋዕት ሲያቀርቡ፣ ወይም ለያህዌ የሚቃጠል መስዋዕት ሲያቀርቡ፣ 19 ተቀባይነትን እንዲያገኝ ከቀንድ ከብታቸው፣ ከበግ ወይም ፍየሎች ውስጥ ነውር የሌለበትን ተባዕት እንስሳ ያቅርቡ፡፡ 20 ነውር ያለበትን ግን አታቅርቡ፡፡ ይህን እኔ አልቀበልም፡፡ 21 ከከብቱ ወይም ከመንጋው ለስዕለት የህብረት መስዋዕት ለያህዌ የሚሰዋ ሁሉ፣ ወይም የበጎ ፍቃድ መስዋዕት የሚያቀርብ ተቀባይነት ያገኝ ዘንድ ነውር የሌለበትን መስዋዕት ያቅርብ፡፡ በእንስሳው ላይ እንከን አይኑርበት፡፡ 22 ዕውር፣ አንካሳ ወይም ሰንካላ፣ ወይም ኪንታሮት፣ ህመም፣ ወይም ቁስል ያለበትን እንስሳ አትሰዉ፡፡ እዚህን በእሳት መስዋዕት አድርጋችሁ በመሰዊያ ላይ ለያህዌ አታቅርቡ፡፡ 23 የበጎ ፈቃድ መስዋዕት አድርጋችሁ ጎደሎ ወይም ትንሽ በሬ ወይም በግ ማቅረብ ትችላላችሁ፣ እንዲህ ያለው መስዋዕት ግን ለስዕለት ተቀባይነት የለውም፣ 24 ለያህዌ ሰንበር ያለበት፣ የተሰበረ፣ የተዘነጠለ፣ ወይም የዘር ፍሬው የተቀጠቀጠ እንስሳ አታቅርቡ፡፡ እነዚህን በምድራችሁ አታቅርቡ፣ 25 ለእግዚአብሔር ለምግብ የሚቀርብ አድርጋችሁ ከመጻተኛው እጅ አትቀበሉ፣ ምክንያቱም በእነዚህ ላይ ጉድለቶች ወይም ነውሮች አሉባቸው እነዚህን ከእናንተ አልቀበለም፡፡›” 26 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 27 “አንድ ጥጃ ወይም አንድ የበግ ወይም የፍየል ግልገል ሲወለድ፣ ከእናቱ ጋር ሰባት ቀናት ይቆይ፡፡ ከዚያም ከስምንተኛው ቀን አንስቶ፣ ለያህዌ በእሳት መስዋዕት ሆኖ መቅረብ ይችላል፡፡ 28 አንዲትን ላም ወይም ሴት በግ ከጥጃዋ ወይም ከግልገሏ ጋር በአንድ ቀን አትረዱ፡፡ 29 ለያህዌ የምስጋና መስዋዕት ስታቀርቡ፣ ተቀባይነት ባለው መንገድ አቅርቡ፡፡ 30 መስዋዕቱ በቀረበበት ቀን ይበላ፡፡ እስከ ማለዳው አንዳች አታስቀሩ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 31 ትዕዛዛቴን ጠብቁ አድርጓቸውም፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 32 ቅዱስ ስሜን አታቃሉ፡፡ በቅድስናዬ በእስራኤል ህዝብ መታወቅ አለብኝ፡፡ እናንተን ለራሴ የለየሁት እኔ ያህዌ ነኝ፣ 33 አምላካችሁ እሆን ዘንድ ከግብጽ ምድር ያወጣኋችሁ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡”



Leviticus 22:1

ቅዱስ ከሆኑ ነገሮች እንደርቁ ንገራቸው

“ቅዱስ ከሆኑ ነገሮች ምን ጊዜ መራቅ እንዳለባቸው ንገራቸው” አንድ ካህን ርኩስ በሆነና ቅዱስ የሆኑ ነገሮች መንካት የሌለበት ሁኔታዎችን እግዚአብሔር ይገልጻል፡፡

ቅዱስ ስሜን እንዳያረክሱ

እዚህ “ማርከስ” የሚለው ቃል አለማክበርን ይገልጻል፡፡ “ስም” የሚለው ቃል የእግዚአብሔርን ባህሪይ ያመለክታል:: አት “ምሥክርነቴን አላከበሩም” ወይም “አላከበሩኝም” ( See Metonymy/ተዛማጅ ባህሪይ የሚቀልጽ ምትክ ቃላት የመጠቀም አነጋገር ዘይቤ ይመልከቱ)

በሚቀጥሉት ትውልዶች

“ከዛሬ/ከአሁን ጀምሮ”

ንጹህ ያልሆነ ሰው

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባው ሰው ንጹህ ያልሆነ ወይም ርኩስ ተበሎአል:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ያ ሰው ከፊቴ ይወገድ

እግዚአብሔርን ማገልገል የማይችል ካህን ብጣሽ ጨርቅ ከልብሰ ወይም ቅርንጫፍ ከዛፍ ተቆርጦ እንደሚወገድ ከእግዚአብሔር መገኘት ተቆርጦ እንደተወገደ ተደርጐ ተገልጾአል፡፡ አት: “ያ ሰው ካህን ሆኖ ማገልገል አይችልም” (ዘይቤይዊ አገላለጽና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 22:4

ተላላፊ የቆዳ በሽታ

ከአንድ ሰው ወደ ሌላው በቀላሉ ሊተላለፍ የሚችል የቆዳ በሽታ ነው

ከሰውነቱ የሚወጣው ፈሳሽ ነገር

“የሰውነት ፈሳሽ ነገር”

ከሰውነቱ

ይህ የሰውን ሀፍረተ አካላት ለዛነት በተሞላ አባባል ይገልጻል፡፡ በዘሌዋዊያን 15 1 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ አት ከሀፍረተ አካላቶች (see Euphemism/ንኣብነት ወይም ለዛ ያለ ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ አንድን ነገር የመግለጽ ዘይቤያዊ አባባል ይመልከቱ)

እስኪነጻ ድረስ

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች የተገባ ሰው ንጹህ ተበሎአል:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ማንኛውን የረከሰውን ነገር የነካ ሰው

እግዚአብሔር ለመንካ ወይም ለመብላት ያልተገባ ያለው አንድ ነገር በአካል ርኩስ ነው:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

አስከሬን በመንካት ደ

“ሙት አካል በመንካት”

ለእግዚአብሔር የቀረቡ መሥዋዕቶች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አንድ ሰው ለእግዚአብሔር ያቀረባቸው መሥዋዕቶች” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ርኩስ የሚያደርገውን በደረቱ የሚሳብ እንስሳ ወይም ርኩስ የሚያደርገውን ሰው ቢነካ

ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት ወይም በደረት የሚሳብ እንስሳ በመንካት ወይም ርኩስ የሆነውን ሰው በመንካት የረከሰ ማንኛውም ሰው (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ካህኑ… ርኩስ ይሆናል

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ያልተገባው ሰው ርኩስ ተብሎአል (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

እስከ ማታ

ጸሐይ እስከሚትጠልቅ

Leviticus 22:7

ንጹህ ይሆናል

ከዚያም ካህኑ ንጹህ ይሆናል ለእግዚአብሔር ዓላማዎች የተገባው ሰው ንጹህ ተብሎአል (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ሞቶ የተገኝ ወይም አውሬ የዘነጠለውን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሞቶ የተገኘውን ወይም አውሬ የገደለውን” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 22:10

አጠቃላይ መረጃ

አሮንና ልጆቹ ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

Leviticus 22:12

ቅዱስ የተዋጽኦ መሥዋዕቶች

“ተዋጽኦ” የሚለው ቃል እንደ ግሥ ሐረግ ሊተረጐም ይችላል:: አት: “ሰዎች ያዋጡት የተቀደሰው መሥዋዕት” (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

Leviticus 22:14

የመሥዋዕቱን አንድ አምስተኛ ጨምሮ ለካህኑ ይተካ

ሁኔኛ ትርጉሞች 1)ምግቡን የበላ ሰው ተመሣሣይ ዓይነት ምግብ ይተካ 2) ስለበላው ምግብ ለካህኑ ገንዘብ ይክፈል አንድ አምስተኛ ከአምስት ተመሣሣይ ክፍሎች አንዱን ማለት ነው:: (ክፍልፋዮችን ይመልከቱ)

ወደ እግዚአብሔር ከፍ አድርገው ያቀረቡትን

እዚህ “ከፍ አድርገው” የሚለው ሀረግ ለእግዚአብሔር አንድን ነገር በአክብሮት የማቅረብ ድርጊታዊ ምልክት ነው:: “ማቅረብ” ከሚለው ጋር በመሠረቱ አንድ ነው :: አት: “አቅርበዋል” (ምልክታዊ ድርጊቶችንና ድርብ ቃላትን/doublet ይመልከቱ)

ቅጣት የሚያስከትል/በደለኛ የሚያደርጋቸውን ኃጢአት እንዳይሸከሙ

ኃጢአት ሰው እንደሚሸከመው ዕቃ ተደርጐ ተገልጾአል ሁኔኛ ትርጉሞች 1) ስለ ኃጢአታቸው ተጠያቂና በደለኛ ይሆናሉ አት ስለሠሩት ኃጢአት በደለኛ ይሆናሉ ወይም 2) ኃጢአት የሚለው ቃል ለሠሩት ኃጢአት ስለሚሰጥ ቅጣት ምትክ ቃል ነው አት በደለኞች ስለሆኑ ቅጣትን ይቀበላሉ:: (ዘይቤያዊ አነጋገርና ምትክ ተመሣሣይ ቃላት ይመልከቱ)

Leviticus 22:17

መጻተኛ

እንግዳ

ተቀባይነት እንዲኖረው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እግዚአብሔር እንዲቀበለው” ወይም “እኔ እግዚአብሔር እንዲቀበለው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 22:20

ተቀባይነት ይኖረው ዘንድ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እኔ እንዲቀበለው” ወይም “እግዚአብሔር እንዲቀበለው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 22:22

ሰባራ ወይም ጉንድሽ

እነዚህ ቃላት በአደጋ ምክንያት የተከሰቱ የአካል ጐደሎነት ያመለክታሉ

እከክ ወይም ቋቁቻ ወይም የማመግል ቁስል

እነዚህ የቆዳ በሽታዎችን ያመለክታሉ

ተቀባይነት አይኖረውም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “አልቀበለውም” ወይም “እግዚአብሔር አይቀበለውም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አካሉ ከመጠን በላይ የረዘመ ወይም ያጠረ

እነዚህ ቃላት በተፈጥሮ ችግር ያለባቸውን እንስሳት ያመለክታሉ

Leviticus 22:24

ለአምላካችሁ ምግብ አድርጋችሁ አታቅርቡ

እዚህ ምግብ አጠቃላይ ምግብ ይወክላል መሥዋዕት ሆነው የቀረቡትን እግዚአብሔር አይበላም:: ካህናት በእግዚአብሔር መሠዊያ መሥዋዕት ያቀርባሉ እናም ከሥጋው ይበላሉ:: አት: “ለእግዚአብሔር እንስሳን እንደምግብ መሥዋዕት አታቅርቡ” (See Synecdoche/ክፍልን እንደ ሙሉ ሙሉን እንደ ክፍል የመግለጽ ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ከባዕዳን እጅ

እጅ የሚለው ቃል መላውን ሰው ይወክላል ባእዳን እንስሳትን በማኮላሸት ለእግዚአብሔር ተቀባይነት እንዳይኖራቸው ስለሚያደርጉ እነርሱ መሥዋዕት አድርገው ለእግዚአብሔር የሚያቀርቡትን እንስሳት እስራኤላዊያን እንዳይጠቀሙ ይገልጻል (see Synecdoche, ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ተቀባይነት አይኖራቸውም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እግዚአብሔር እነዚህን ከእናንት አይቀበልም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 22:26

ተቀባይነት ያለው ይሆናል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሊትቀበሉት ትችላላችሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ለሚቃጠል መሥዋዕት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 22:28

ይበላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ብሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

መሥዋዕት ሆኖ ቀርቦአል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “መሥዋዕት አድርጋችሁ አቅርባችኋል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 22:31

ትእዛዛቴን ጠብቁ አድርጓቸውም

“ጠብቁ” እና “አድርጉ” የሚሉ ቃላት ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: ሕዝቡ የእግዚአብሔርን ሕጐች እንዲታዘዙ ትኩረት የሚሰጡ ናቸው:: አት: “ሕጐቼን ታዘዙ” (See Doublet/ ተመሣሣይ ትርጉም ያላቸውን ድርብ ቃላትን ይመልከቱ)

ቅዱስ ስሜን አታርክሱ

እዚህ “ስም” የሚለው ቃል እግዚአብሔርንና ምሥክርነቱን ይወክላል፤ እናም “ማርከስ” ማለት እግዚአብሔር ፈጣሪና የዓለም ሁለ አምላክ በመሆኑ የሚገባውን ክብር አለመስጠት ነው:: (ተዛማጅ ባህርይ የሚገልጹ ምትክ ቃላት አጠቃቀም ዘይቤ ይመልከቱ/See Metonymy)

እኔ ቅዱስ መሆነ በእስራኤላዊያን ዘንድ ሊታወቅ ይገባል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እስራኤላዊያን ቅዱስ መሆነን ማወቅ አለባቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)


Chapter 23

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “ለእስራኤል ህዝብ እንዲህ በላቸው፣ ‹ለያህዌ የተለዩ የተቀደሱ ባዕሎቻችሁ፣ እንደ ቅዱስ ጉባኤዎቻችሁ የምታውጇቸው፣ የእኔ መደበኛ በዓላት ናቸው፡፡ 3 ስድስት ቀናት ትሰራላችሁ፣ ሰባተኛው ቀን ግን ሙሉ እረፍት የሚደረግበት ሰንበት ነው፣ የተቀደሰ ጉባኤ ዕለት ነው በምትኖሩበት ስፍራ ሁሉ ለያህዌ ሰንበት ስለሆነ ምንም ስራ አትስሩበት፡፡ 4 እነዚህ ለያህዌ የተመረጡ በዓላት ብላችሁ በተወሰነላቸው ጊዜ የምታውጇቸው የተቀደሱ ስብሰባዎች ናቸው፡፡ 5 በመጀመሪያው ወር በወሩ በአስራ አራተኛው ቀን ጸሀይ ስትጠልቅ የያህዌ ፋሲካ ነው፡፡ 6 በዚያው ወር በአስራ አምስተኛው ቀን የያህዌ የቂጣ በዓል ነው፡፡ ለሰባት ቀናት እርሾ ያልገባበት ቂጣ ትበላላችሁ፡፡ 7 በመጀመሪያው ቀን ለያህዌ የተለየ ጉባኤ ይኖራችኋል፣ የተለመደ ተግባራችሁን አትሰሩበትም፡፡ 8 ለሰባት ቀናት በእሳት የሚቀርብ መስዋዕት ለያህዌ ታቀርባላችሁ ሰባተኛው ቀን የተለመደ ተግባራችሁን የማታከናውኑበት ለያህዌ የተለየ ጉባኤ የሚደረግበት ነው›” 9 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 10 ”ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ ብለህ ንገራቸው ‹ወደምሰጣችሁ ምድር ስትገቡ፣ እና የመጀመሪያውን አዝመራ ስትሰበስቡ፣ ከበኩራቱ ፍሬዎች ለካህኑ አንድ ነዶ ታመጣላችሁ፡፡ 11 ነዶው ተቀባይነትን እንዲያገኝ ካህኑ በያህዌ ፊት ይወዘውዘውና ለእርሱ ያቀርበዋል፡፡ ካህኑ ነዶውን የሚወዘውዘውና ለእኔ የሚያቀርበው በሰንበት ቀን ማግስት ነው፡፡ 12 ነዶውን በምትወዘውዙበትና ለእኔ በምታቀርቡበት ቀን ለያህዌ ነውር የሌለበት የአንድ አመት ወንድ ጠቦት የሚቃጠል መስዋዕት ታቀርባላችሁ፡፡ 13 የእህል ቁርባን ለያህዌ መልካም መዓዛ የሚሆን በዘይት የተለወሰ የኢፍ ሁለት አስረኛ መልካም ዱቄት፣ በእሳት የተዘጋጀ መስዋዕት፣ እና ከነዚህም ጋር የኢን አንድ አራተኛ ወይን የመጠጥ ቁርባን መቅረብ አለበት፡፡ 14 ለአምላካችሁ ይህን መስዋዕት እስከምታቀርቡበት ቀን ድረስ ምንም ዓይነት ዳቦ፣ አሊያም የተጠበሰ እሸት ወይም ለምለሙን እሸት አትብሉ፡፡ ይህ ለትወልዳችሁ ሁሉ በምትኖሩበት ስፍራ ሁሉ ቋሚ መታሰቢያ ይሆናል፡፡ 15 ከዚያ ሰንበት ቀን ማግስት አንስቶ ነዶውን ለመወዝወዝና ለያህዌ ለማቅረብ ካመጣችሁት ቀን ጀምራችሁ ሰባት ሙሉ ሳምንታት፣ ሰባት ሰንበት ትቆጥራላችሁ፣ 16 እስከ ሰባተኛው ሰንበት ማግስት ድረስ ትቆጥራላሁ፡፡ ያም ማለት ሀምሳ ቀናት ትቆጥራላችሁ፡፡ ከዚያ ለያህዌ የአዲስ አዝመራ መስዋዕት ታቀርባላችሁ፡፡ 17 ከየቤቶቻችሁ ከኢፍ ሁለት አስረኛ የተጋገሩ ሁለት ዳቦዎች ታመጣላችሁ፡፡ ከመልካም ዱቄት የሚዘጋጅና በእርሾ የተጋገሩ ይሁኑ፤ ከበኩራት ፍሬዎች የሚቀርቡ የሚወዘወዙና ለያህዌ የሚቀርቡ መስዋዕቶች ይሆናሉ፡፡ 18 ከዳቦው ጋር ነውር የሌለባቸው የአንድ ዓመት እድሜ ያላቸው ሰባት ጠቦቶች፣ አንድ ወይፈን በሬ፣ እና ሁለት አውራ በጎች ታቀርባላችሁ፡፡ እነርሱም ለያህዌ የሚቃጠል መስዋዕት ይሆናሉ፣ ከእህል ቁርባን ከመጠጥ ቁርባን ጋር፣ በእሳት የተዘጋጀ መስዋዕት እና ለያህዌ መልካም መዓዛ ያለው መስዋዕት ይሆናሉ፡፡ 19 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ታቀርባላሁ፣ እንዲሁም ለህብረት መስዋዕት የአንድ አመት ዕድሜ ያላቸው ሁለት ወንድ ጠቦቶች ለመስዋዕት ታቀርባላችሁ፡፡ 20 ካህኑ ከበኩራት ፍሬዎች ዳቦ ጋር በያህዌ ፊት ይወዘወዛቸው፣ እነርሱንም መስዋዕት አድርጎ ለእርሱ ከሁለት ጠቦቶች ጋር ያቅርብ፡፡ ለያህዌ ቅዱስ መስዋዕቶች ሲሆኑ የካህኑ ድርሻ ናቸው፡፡ 21 በዚያው ቀን ማወጅ አለባችሁ፡፡ የተቀደሰ ጉባኤ ይኖራል፣ እናም የተለመደ ስራችሁን አትሰሩም፡፤ ይህ የህዝባችሁ በትውልዶች ሁሉ በምትኖሩበት ሥፍራ ሁሉ ቋሚ መታሰቢያ ይሆናል፡፡ 22 የምድራችሁን ፍሬ ስትሰበስቡ፣ የእርሻችሁን ጥግጋት ሁሉ ሙሉ ለሙሉ አትሰብስቡ፣ የሰብላችን ቃርሚያ ሁሉ አትሰብስቡ፡፡ እነዚህን ለድሆችና ለመጻተኛው ተዉላቸው፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡” 23 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 24 ”ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‹በሰባተኛው ወር፣ የወሩ የመጀመሪያው ቀን ለእናንተ ታላቅ እረፍት ይሆናል፣ በመለኮት ድምጽ መታሰቢያ የሚደረግበት፣ እና የተቀደሰ ጉባኤ ይሆናል፡፡ 25 የተለመደ ሥራ አትሰሩበትም፣ ለያህዌ የእሳት መስዋዕት አቅርቡበት፡፡›” 26 ከዚያ ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 27 “አሁን የዚህ የሰባተኛው ወር አስረኛ ቀን የስርየት ቀን ይሆናል፡፡ ለያህዌ የተለየ ጉባኤ መሆን አለበት፣ ራሳችሁን ማዋረድና ለያህዌ በእሳት መስዋዕት መሰዋት አለባችሁ፡፡ 28 በዚያን ቀን ምንም ሥራ አትስሩ ምክንያቱም በአምላካችሁ በያዌ ፊት ለራሳች ማስታሰርያ የምታቀርቡበት የስርየት ቀን ነው፡፡ 29 በዚያን ቀን ራሱን የማያዋርድ ማንም ቢሆን ከህዝቡ ተለይቶ ይጥፋ፡፡ 30 በዚያን ቀን ማናቸውንም ሥራ የሚሰራውን ማንንም ቢሆን፣ እኔ ያህዌ ከህዝቡ መሀል አጠፋዋለሁ፡፡ 31 በዚያ ቀን ማናቸውንም ዐይነት ሥራ አትሰሩም፡፡ ይህ በህዝባችሁና ትውልዶቻችሁ ሁሉ በምትኖሩባቸው ስፍራዎች ሁሉ ቋሚ መታሰቢያ ይሆናል፡፡ 32 ይህ ቀን ለእናንተ የከበረ የሰንበት ዕረፍት ይሁንላችሁ፣ እናንተም በወሩ በዘጠነኛው ቀን ራሳችን አዋርዱ፡፡ ከምሽት እስከ ምሽት ሰንበትን ጠብቁ፡፡” 33 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 34 “ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‹በሰባተኛው ወር አስራ አምስተኛው ቀን ለያህዌ የዳስ በዓል ይሆናል፡፡ ይህም ሰባት ቀናት ይወስዳል፡፡ 35 በመጀመሪያው ቀን ቅዱስ ጉባኤ ይኖራል፡፡ የተለመደውን ሥራ አትስሩበት፡፡ 36 ለሰባት ቀናት ለያህዌ የሚቃጠል መስዋዕት አቅርቡበት፡፡ በስምንተኛው ቀን ቅዱስ ጉባኤ ይሁን፣ እናንተም ለያህዌ የሚቃጠል መስዋዕት አቅርቡ፡፡ ይህ ክቡር ጉባኤ ነው፣ እናም አንዳች የተለመደ ሥራ አትስሩበት፡፡ 37 እነዚህ ለያህዌ የተለዩ በአላት ናቸው፣ ለያህዌ የሚቃጠል መስዋዕት ለማቅረብ ቅዱስ ጉባኤ የምታውጁበት፣ የሚቃጠል መስዋዕትና የእህል ቁርባን፣ የመስዋዕቶችና የመጠጥ ቁርባች እያንዳንዱን በየራሱ ቀን ለይታችሁ ለእግዚአብሔር የምታውጁባቸው በዓላት ናቸው፡፡ 38 እነዚህ በአላት ከያህዌ ሰንበታትና ከእናንተ ስጦታዎች ተጨማሪ ናቸው፣ ስጦቻችሁ ሁሉ፣ እና ለያህዌ የምትሰጧቸው የበጎ ፈቃድ መስዋዕቶቻችሁ ሁሉ ናቸው፡፡ 39 የዳስ በዓልን በሚመለከት፣ በሰባተኛው ወር በአስራ አምስተኛው ቀን፣ እናንተ የምድሪቱን ፍሬዎች ስትሰበስቡ ይህን የያህዌ በዓል ለሰባት ቀናት ማክበር አለባችሁ፡፡ የመጀመሪያው ቀን የፍፁም ዕረፍት ቀን ይሆናል፣ ስምንተኛው ቀንም እንደዚሁ የፍጹም ዕረፍት ቀን ይሆናል፡፡ 40 በመጀመሪያው ቀን ከዛፎቹ መልካሞቹን ፍሬዎች ውሰዱ፣ የዘንባባ ዛፎች ዝንጣፊዎች፣ እና የለምለሙ ዛፎች ቅርንጫፎች፣ ከወንዝ ዳርቻ ለምለም ዛፎች ቅርንጫፎች ወስዳችሁ በአምላካችሁ በያህዌ ፊት ለሰባት ቀናት ሃሴት ታደርጋላችሁ፡፡ 41 በየአመቱ ለሰባት ቀናት፣ ይህን በዓል ለያህዌ ታከብራላችሁ፡፡ ይህ በትውልዳችሁ ሁሉ በምትኖሩባቸው ስፍራዎች ሁሉ ቋሚ መታሰቢያ ይሆናል፡፡ ይህን በዓል በሰባተኛው ወር አክብሩ፡፡ 42 ለሰባት ቀናት በትንንሽ ዳሶች ውስጥ ትኖራላችሁ፡፡ እስራኤላዊ የሆነ ሁሉ ለሰባት ቀናት በትንንሽ ዳሶች ውስጥ ይቀመጥ፣ 43 ከእናንተ በኋላ የሚመጣው ትውልድ፣ የልጅ ልጆቻችሁ፣ እስራኤላውያንን ከግብጽ ምድር ሳወጣ በእንደዚህ ዐይነት ዳሶች ውስጥ እንዴት እንዲኖሩ እንዳደረግኩ ያውቃሉ፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡›” 44 በዚህ መንገድ፣ ሙሴ ለእስራኤል ህዝብ ለያህዌ የተለዩትን በዓላት አስታወቁ፡፡



Leviticus 23:1

ለእግዚአብሔር የተቀደሱ በዓላት

እነዚህ እግዚአብሔር ቀን የመደበላቸው በዓላት ናቸው፡፡ በእነዚህ በዓላትሕዝቡ እርሱን ያመልካል፡፡ አት፡ “ለእግዚአብሔር የሆኑ በዓላት” ወይም “የእግዚአብሔር በዓላት”

Leviticus 23:3

አጠቃላይ መረጃ

በተለዩ ቀናትና ጊዜያት ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ሰባተኛው ቀን የዕረፍት ሰንበት ነው

ይህ ሕዝቡ መለማመድ ያለበት ነው ስድስት የሥራ ቀናት በኋላ በሰባተኛው ቀን ማረፍ አለባቸው

የተቀደሰ ጉባዔ

በዚያ ቀን እግዚአብሔርን ለማምለክ ሕዝቡ እንዲሰበሰብ የተፈለገው ያ ቀን የስብሰባ እንደሆነ ተደርጐ ተገልጾአል:: አት “የተቀደሰ ቀን፤ በአንድነት እኔን ለማምለክ የሚትሰባሰቡበት ጊዜ”

Leviticus 23:4

በተወሰነው ጊዜ

“በመደበኛው ጊዜ”

የመጀመሪያው ወር አሥራ አራተኛው ቀን በዚያ ወር በአሥራ አምሰተኛው ቀን

በዕብራዊያን የቀን አቆጣጠር የመጀመሪያ ወር እግዚአብሔር እስራኤላዊያንን ከግብጽ ያመለክታል አሥራ አራተኛው ቀንና አሥራ አምስተኛው ቀን በምዕራባዊያን አቆጣጠር በሚያዝያ ወር መግቢያ ናቸው:: (የእብራይጥ ወራትና ተራ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ምሽት

ጸሐይ ስጠልቅ

Leviticus 23:7

በመጀመሪያው ቀን የተቀደሰ ጉባዔ አድርጉ

“መጀመሪያውን ቀን ጉባዔ ለማድረግ ለዩ” ወይም “የመጀመሪያውን ቀን እንደ ልዩና የጉባዔ ቀን ቁጠሩት”

የሚቃጠል መሥዋዕት አቅርቡ

በመሠዊያው በማቃጠል ለእግዚአብሔር ያቀርቡታል

ሰባተኛው ቀን ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ጉባዔ ነው

በዚያ ቀን እግዚአብሔርን ለማምለክ ሕዝቡ እንዲሰበሰብ የተፈለገው ያ ቀን የስብሰባ እንደሆነ ተደርጐ ተገልጾአል:: ለእግዚአብሔር የተቀደሰ/የተለየ ማለት በሚሰባሰቡበት ጊዜ እግዚአብሔርን ያመልኩታል ማለት ነው:: አት: “ሰባተኛው ቀን በአንድነት ተሰባስባችሁ እግዚአብሔርን የሚታመልኩበት ቀን ነው”

Leviticus 23:9

ተቀባይነት እንዲያገኝላችሁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እግዚአብሔር እንዲቀበልላችሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 23:12

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ

አንድ ኢፍ 22 ሊትር ነው:: አት: አራት ከግማሽ ሊትር (መጽሐይ ቅዱሳዊ መለኪያዎችን ይመልከቱ)፡፡

አንድ አራተኛ የኢን መሥፈሪያ

አንድ ኢን 3.7 ሊትር ነው:: አት: አንድ ሊትር መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎችን ይመልከቱ::

ቈሎ ወይም እሸት ጥራጥሬ አይሁን

የተቀቀለ ወይም ያልተቀቀለ ጥራጥሬ አይሁን ይህም ለሚመጡት ትውልዶች የዘላለም ሥርዓት ነው:: ይህም እነርሱ ሆነ ቀጣይ ትውልዳቸው ይህን ሥርዓት ለዘላለም መጠበቅ አለባቸው ማለት ነው በዘሌዋዊያን 3:17 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Leviticus 23:15

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ሃምሣ ቀናት

“5ዐ ቀናት” ተራ ቁጥሮችን ይመልከቱ

ሰባተኛ

ይህ ቁጥር 7 መደበኛ ስያሜ ነው (መደበኛ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

Leviticus 23:17

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

በሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ የላመ ዱቄት በእርሾ የተጋገረ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ያም ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ የላመ ዱቄት ወስዳችሁ በእርሾ የጋገራችሁት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ

በግምት 4.5 ሊትር ያህላል:: አት: አራት ከግማሽ ሊትር (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር መልካም መዓዛ ይሰጣል

በመልካም በዓዛው የእግዚአብሔር መደሰት መሥዋዕቱን በሚያቃጥለው ሰው መደሰትን ይወክላል:: አት: “እግዚአብሔር ይደሰትባችኋል” ወይም “እግዚአብሔርን ያስደስተዋል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 23:19

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

Leviticus 23:22

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

የምድራችሁን መከር በምትሰበስቡበት ጊዜ የእርሻችሁን ዳርና ዳር አትጨዱ

አት: “መከር በምትሰበስቡበት ጊዜ እስከ እርሻችሁ ዳርና ዳር ድረስ ያለውን ሁሉ አትሰብስቡ”

Leviticus 23:23

ሰባተኛው ወር በወሩም መጀመሪያው ቀን

ይህ በዕብራዊያን ቀን አቆጣጠር ሰባተኛ ወር ነው:: መጀመሪያው ቀን በምዕራባዊያን አቆጣጠር መስከረም ወር አጋማሽ አካባቢ ነው:: (የዕብራይስጥ ወራትንና መደበኛ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

እረፍት ይሁንላችሁ

ለሥራ ሳይሆን ለአምልዕኮ ብቻ የተመደበ ጊዜ ማለት ነው

መሥዋዕትን በእሳት ለእግዚአብሔር አቅርቡ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ለእግዚአብሔር መሥዋዕትን በእሳት አቅርቡ” ወይም “ለእግዚአብሔር በመሠዊያው መሥዋዕትን አቃጥሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 23:26

የሰባተኛው ወር አሥረኛ ቀን

ይህ በዕብራዊያን ቀን አቆጣጠር ሰባተኛ ወር ነው:: በምዕራባዊያን አቆጣጠር አሥረኛው ቀን መስከረም ወር መጨረሻ አካባቢ ነው:: (የዕብራይስጥ ወራትንና መደበኛ ቁጥሮችን ይመልከቱ)

የሥርየት ቀን

የእስራኤልን ሕዝብ ኃጢአት ሁሉ እግዚአብሔር ይቅር እንዲል በየዓመቱ በዚህ ቀን ሊቀ ካህኑ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት ያቀርባል:: አት፡ “ለይቅርታ ወይም ለሥርየት መሥዋዕት የሚቀርብበት ቀን” (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Leviticus 23:28

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

በየዓመቱ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ከወገኖቹ መካከል ተለይቶ ይጥፋ

መገለል እንደ መቆረጥ ተነግሮአል በዘሌዋዊያ 7:2ዐ ይህን ሀሳብ እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ:: አት: “ከሕዝቡ ዘንድ መወገዝ አለበት” ወይም “ ሰውየውን ከሕዝቡ መለየት አለባችሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገርና ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 23:30

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

በየዓመቱ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

በዚያ ዕለት

“በሥርየት ቀን”

ይህም ለሚመጡት ትውልዶች የዘላለም ሥርዓት ነው::

ይህም እነርሱ ሆነ ቀጣይ ትውልዳቸው ይህን ሥርዓት ለዘላለም መጠበቅ አለባቸው ማለት ነው፡፡ በዘሌዋዊያን 3:17 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

የዕረፍት ሰንበት

ይህ በየሳምንቱ በሰባተኛው ቀን እንደሚከበረው ሰንበት አይደለም፡፡ ይህ በሥርየት ቀን የሚከበር ልዩ ሰንበት ነው፡፡

ራሳችሁን ዝቅ ዝቅ አድርጉ

በዚህ ዐውድ ራሳቸውን ዝቅ ማድረግ ማንኛውን ምግብ አለመብላታቸውን ያመለክታል ይህ ግልጽ ሆኖ ሊነገር ይችላል:: አት: “ራሳችሁን ዝቅ አድርጉ ምግብንም አትብሉ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በወሩም ዘጠነኛው ቀን

ይህ በዕብራይስጥ ቀን መቁጠሪያ ሰባተኛ ወር ነው በምዕራባዊያነ ቀን መቁጠሪያ ዘጠነኛው ቀን መስከረም ወር መጨረሻ አካባቢ ነው ይህም ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት የሰባተኛው ወር ዘጠነኛ ቀን (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ከምሽት እስከ ምሽት

ከጸሐይ መግቢያ እስከሚቀጥለው ቀን ጸሐይ መግቢያ

Leviticus 23:33

ሰባተኛው ወር በገባ በአሥራ አምስተኛው ቀን

x

Leviticus 23:35

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ስለ ዳስ በዓል መመሪያዎችን ያስተላልፋል

Leviticus 23:37

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

ሕዝቡ በየዓመቱ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

እነዚህ መደበኛ በዓላት ናቸው

በ23: 1-36 የተጠቀሱ በዓላትን ነው::

Leviticus 23:40

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር የዳስ በዓል መመሪያዎችን ያስተላልፋል

የዘንባባ ዝንጣፊ…የአኻያ ዛፍ ቅርንጫፍ

እነዚህ ቅርጫፎች የሚጠቅሙት 1) ጊዜያዊ ዳስ ለመሥራት 2) የበዓላቸውን ደስታ በማውለብለብ አንዳንድ ትርጉሞች እነዚህን ጥቅሞች ግለጽ አድርገው ሲገልጹ ሌሎች ግን ግልጽ ሳያደርጉ ይተዋሉ:: (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የአኻያ ዛፎች

በውሃ አጠገብ የሚበቅሉ ረጅ ቀጭን ቅጠሎች ያሉአቸው ተክሎች ወይም ዛፎች ናቸው (ያልታወቁትን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

Leviticus 23:42

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር የዳስ በዓል መመሪያዎችን ያስተላልፋል

ትውልዳችሁ… የልጅ ልጆቻችሁ ያውቃሉ

“የልጅ ልጆቻችሁ” ከአንድ ትውልድ ቀጥሎ የሚኖር እያንዳንዱን ትውልድ የሚገልጽ ፈሊጣዊ አባባል ነው: አት: “ትውልዳችሁ የሚመጣው ትውልድ ሁሉ ያውቃሉ ወይም ትውልዳችሁ ሁሉ ለዘላለም ያውቃል” (ፈሊጣዊ አባባሎች ይመልከቱ)


Chapter 24

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “የእስራኤል ሰዎች መቅረዞች ሁልጊዜም እንዲነዱና ብርሃን እንዲሰጡ ከወይራ ፍሬ የተጠመቀ ንጹኅ ዘይት ለመቅረዞችህ ወደ አንተ እንዲያመጡ እዘዛቸው፡፡ 3 አሮን ያለማቋረጥ ከምሽት እስከ ማለዳ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ከመጋረጃው ውጭ በቃልኪዳኔ ድንጋጌ ፊት መቅረዙን በያህዌ ፊት ያለማቋረጥ ያብራ፡፡ ይህ በትወልዳች ሁሉ ቋሚ ስርዓት ይሆናል፡፡ 4 ሊቀ ካህኑ በንጹኅ ወርቅ በተሰራው የመቅረዝ መያዣ ላይ መቅረዞቹ ሁልጊዜም በያህዌ ፊት እንዲበሩ ያደርጋል፡፡ 5 መልካም ዱቄት ወስደህ አስራ ሁለት ዳቦዎች ጋግር፡፡ ለእያንዳንዱ ዳቦ የኢፍ ሁለት እስረኛ መጠን ተጠቀም፡፡ 6 ከዚያ በሁለት ረድፍ ደርድራቸው፣ በአንዱ መስመር ስድስቱን በንጹኅ ወርቅ በተሰራ ጠረጴዛ ላይ በያህዌ ፊት ደርድር፡፡ 7 በእያንዳንዱ የዳቦዎቹ ረድፍ እንደ ዳቦዎቹ ምልክት ንጹኅ ዕጣን አድርግበት፡፡ ይህ ዕጣን ለያህዌ በእሳት የሚቀርብ መስዋእት ይሆናል፡፡ 8 በእያንዳንዱ የሰንበት ዕለት ሊቀ ካህኑ የእስራኤልን ህዝብ ወክሎ የዘላለም ቃልኪዳን ምልክት አድርጎ ህብስቱን በመደበኛነት ለያህዌ ያቀርባል፡፡ 9 ይህ መስዋዕት የአሮንና የልጆቹ ድርሻ ይሆናል፡፡ ሙሉ ለሙሉ ለእርሱ የተለየና ለያህዌ በእሳት ከሚቀርበው መስዋዕት የተወሰደ ስለሆነ ቅዱስ በሆነው ስፍራ ይብሉት፡፡” 10 እናቱ እስራኤላዊ የሆነች እና አባቱ ግብፃዊ የሆነ ልጅ በእስራኤል ህዝብ መሀል ወጣ፡፡ ይህ እስራኤላዊት ሴት ልጅ በሰፈር ውስጥ ከእስራኤላዊ ሰው ጋር ተጣላ፡፡ 11 የእስራኤላዊቷ ሴት ልጅ የያህዌን ስም ሰደበ እግዚአበሔርንም ረገመ፣ ስለዚህም ህዝቡ ወደ ሙሴ አመጡት፡፡ የእናቱ ስም ሰሎሚት ነበር፣ የደብራይ ልጅ ስትሆን ከዳን ወገን ነበረች፡፡ 12 ያህዌ ራሱ ፈቃዱን እስኪገልጽላቸው ድረስ በጥበቃ ስር አቆዩት፡፡ 13 ከዚያ ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 14 “እግዚአብሔርን የተሳደበውን ሰው ከሰፈር አውጡት የሰሙት ሁሉ እጆቻቸውን በላዩ ይጫኑ፣ ከዚያም መላው ጉባኤ በድንጋይ ይውገረው፡፡ 15 ለእስራኤል ሰዎች ብለህ ግለጽላቸው፣ ‹አምላኩን የተሳደበ ማንኛውም ሰው በደሉን ይሸከም፡፡ 16 ተወላጅ የሆነ እስራኤላዊም ቢሆን ወይም መጻተኛ የያህዌን ስም በስድብ ያቃለለ መላው ጉባኤ በድንጋይ ይውገሩትና ይገደል፡፡ ማንም ሰው የያህዌን ስም ቢሳደብ፣ ይገደል፡፡ 17 ሌላ ሰው የገደለ ይገደል፡፡ 18 የሌላውን ሰው እንስሳ የገደለ በገደለው ፈንታ ይክፈል፣ ህይወት ስለ ህይወት ነው፡፡ 19 አንድ ሰው ጎረቤቱን ቢጎዳ፣ እርሱ በጎረቤቱ ላይ ያደረገው ነገር ይደረግበት፡፡ 20 ስብራት ስለ ስብራት፣ አይን ስለ አይን፣ ጥርስ ስለ ጥርስ፡፡ በአንድ ሰው ላይ ጉዳት እንዳደረሰ፣ በእርሱም ላይ እንደዚያው ይደረግበት፡፡ 21 ማንም እንስሳ የገደለ ሰው መልሶ ይክፈል ማንም ሰው የገደለ ይገደል፡፡ 22 ለመጻተኛውም ይሁን ለተወላጅ እስራኤላዊው አንድ አይነት ህግ ይኑራችሁ፣ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝና፡፡” 23 ሙሴ ለእስራኤል ሰዎች ይህን ነገራቸው፣ ሰዎቹም ያህዌን የተሳደበውን ሰው ከሰፈር ውጭ አመጡት፡፡ በድንጋይ ወገሩት፡፡ የእስራኤል ሰዎች የያህዌን ትዕዛዝ ሙሴ ባዘዘው መሠረት ፈጸሙ፡፡



Leviticus 24:1

አጠቃላይ መረጃ

በመገናኛ ድንኳን ስላሉ ነገሮች እግዚአብሔር ለሙሴ መመሪያ ይሰጣል

ከወይራ ተጨምቆ የተጠለለ ዘይት

“ንጹህ የወይራ ዘይት”

መብራት

ለእግዚአብሔር በተቀደሰው መገናኛ ድንኳን ያለውን መብራት ያመለክታል:: ይህም ግልጽ መደረግ አለበት:: አት: “በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያለው መብራት” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 24:3

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

በመገናኛ ድንኳን ስላሉ ነገሮች እግዚአብሔር ለሙሴ መመሪያ መስጠቱን ይቀጥላል

ከምስክሩ መጋረጃ ውጭ በእግዚአብሔር ፊት

“የኪዳን ምሥክር” የሚለው ሀረግ ሕግጋት የተጻፉባቸው ጽላቶች ወይም ጽላቶች የተቀመጡበት ሣጥን ያመለክታል:: እነዚህም በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ከመጋረጃው በስተጀርባ ባለው እጅግ የተቀደሰ ቦታ በሆነው ክፍል ይቀመጣሉ፡፡ አት: “ከመጋጃው ውጭ በምስክሩ ጽላቶች ፊት” ወይም “ከመጋረጃው ውጭ በኪዳኑ ሣጥን ፊት” (See Synecdoche/ ክፍል ሙሉን እንደሚወክል እናም ሙሉ ክፍልን እንደሚወክል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

መጋረጃው

በግድግዳ ላይ የሚንጠልጠል ወፍራም ጨርቅ ነው:: እንደመስኮት መጋረጃዎች ስስ አይደለም::

ከምሽት እስከ ጥዋት

“ከጸሐይ ጥልቀት እስከ ጸሐይ መውጣት” ወይም “ሌሊቱን ሙሉ”

ይህም ለሚመጡት ትውልዳችሁ የዘላለም ሥርዓት ነው::

ይህም እነርሱ ሆነ ቀጣይ ትውልዳቸው ይህን ሥርዓት ለዘላለም መጠበቅ አለባቸው ማለት ነው፡፡ በዘሌዋዊያን 3:17 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Leviticus 24:5

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

በመገናኛ ድንኳን ስላሉ ነገሮች እግዚአብሔር ለሙሴ መመሪያ መስጠቱን ይቀጥላል

ሁለት አሥረኛ የኢፍ መስፈሪያ

4.5 ሊትር ያህላል:: አት አራት ከግማሽ ሊትር (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎች ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ፊት ባለው ንጹህ ወርቅ ጠረጴዛ

ይህ ጠረጴዛ በቅዱስ ቦታ ነው ማለትም ከቅድስተ ቅዱሳኑ ፊት ነው

Leviticus 24:7

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

በመገናኛ ድንኳን ስላሉ ነገሮች እግዚአብሔር ለሙሴ መመሪያ መስጠቱን ይቀጥላል

ንጹህ ዕጣን በኀብስቱ በእያንዳንዱ ረድፍ ላይ አኑር

ዕጣኑ በኀብስቱ ላይ ሳይሆን በየረድፉ በተቆራረሱ ጐን ሊሆን ይችላል አት ንጹህ ዕጣን በየረድፉ በተቆራረሱ አጠገብ አኑር (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የመታሰቢያ ድርሻ ሆኖ የሚቀርብ መስዋዕት

ዕጣኑ ምን እንደሚወክል መገለጽ አለበት አት: “እያንዳንዱ የተቆራረሰው የኀብስቱ አካለ መስዋዕት እንደሆነ ይወክላል” ወይም “የተቆራረሱ አካላት መሥዋዕት መሆናቸውን ይወክላል”

ይህም ዕጣን በእግዚአብሔር ፊት ይጤስ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ለእግዚአብሔር ዕጣኑን አጢሱ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ይህ መሥዋዕት

“መሥዋዕት ሆኖ የቀረበው ይህ ኀብስት”

ከሚቀርበው መሥዋዕት ድርሻቸው ነው

“ከሚቀርበው መሥዋዕት ሊወስዱት የማችሉት”

ለእግዚአብሔር በእሳት የሚቀርቡ መሥዋዕቶች

“ለእግዚአብሔር የሚቃጠሉ መሥዋዕቶች” ወይም “ለእግዚአብሔር የሚታቃጥሉአቸው መሥዋዕቶች”

Leviticus 24:10

እንዲህ ሆነ

ይህ ሀረግ በመጽሐፉ አድስ ክፍል መጀመሩን ያመለክታል

የእግዚአብሔርን ስም አቃለለ ሰደበም

ሁለቱ ሀረጐች በመሠረቱ ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: አት: “እግዚአብሔርን በመስደብ አቃለለ” ወይም “ስለእግዚአብሔር ክፉ ነገር ተናገረ” ተመሣሣይ ንጽጽር ይመልከቱ::

ሰሎሚት

የሴትየዋ ስም ነው:: ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ::

ደብራይ

የሰውየው ስም ነው:: ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ::

Leviticus 24:13

የሰሙት ሁሉ እጃቸውን በራሱ ላይ ይጫኑበት

ሰውየው በደለኛ ሰለመሆኑ ለማሣወቅ እጃቸውን በራሱ ላይ ይጫኑበት:: (ምልክታዊ ድርጊቶችን ይመልከቱ)

Leviticus 24:15

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

እግዚአብሔርን በረገመው ሰው ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገር ቀጠለ

የራሱን በደል ይሸከማል

ስለኃጢአቱ የሚሠቃየው በደሉን እንደተሸከመ ተደርጐ ተነግሮአል:: አት: “ስለኃጢአቱ ይሠቀይ” ወይም “ይቀጣ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በእርግጥ ይገደል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሕዝቡ ይግደለው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 24:17

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

አንድ ሰው አንድን መጥፎ ነገር ቢያደርግ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

እርሱ መገደል አለበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሰውን የገደለ ሰው ግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ካሣውን ይክፈል

እንዴት ካሣውን መክፈል እንዳለበት ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “ሕይወት ያለውን ያንኑ ዓይነት እንስሳ በመስጠት ይተካ” (ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሕይወት ለሕይወት ፈንታ

የአንዱ ሕይወት የሌላኛውን እንደሚተካ የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው አት የአንድ ሕይወት የሌላኛውን ይተካ (ፈሊጣዊ አገላለጽ ይጠቀሙ)

Leviticus 24:19

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

አንድ ሰው አንድን መጥፎ ነገር ቢያደርግ ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

የዚያው ዓይነት ጉዳት ይፈጸምበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የዚያው ዓይነት ጉዳት ፈጽሙበት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በስብራት ፈንታ ስብራት በዐይን ፈንታ ዐይን በጥርስ ፈንታ ጥርስ

አነዚህ ሀረጐች አጽንዖት የሚሰጡት አንድ ሰው በሌላው ሰው ያደረሰበትን ጉዳት ተመሣሣይ ዓይነት ጉዳት በቅጣት እንዲቀበል ነው

በስብራት ፈንታ ስብራት

ይህ የተሠበሩ አጥንቶችን ያመለክታል:: አት: “በተሠበረው አጥንት ፈንታ የአጥንት ስብራት” ወይም “የአንድን ሰው አጥንት ሰብሮ እንደሆነ አጥንቱ ይሰበር” ወይም “የአንድን ሰው አጥንት ሠብሮ እንደሆን ከእርሱ አጥንቶች አንዱን ይስበሩ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በዓይን ፈንታ ዓይን

ይህ ዓይን እንዲጐዳ ወይም እንዲወገድ ያመለክታል:: “የአንድን ሰው አይን አጥፍቶ እንደሆነ ከአይኖቹ አንዱ ይወገድ” ወይም “የአንድን ሰው አይን አጥፍቶ እንደሆነ ከእርሱ ዓይኖች አንዱን ያጥፉ” (ፈሊጣዊ አባባል ይመልከቱ)

በጥርስ ፈንታ ጥርስ

ይህ የሚያመለክተው ጥርስን ከአገጭ መትቶ ማስወጣት ማለት ነው:: አት: “የአንድን ጥርስ አውልቆ ከሆነ ከጥርሶቹ አንድ ይውለቅ” ወይም “የአንድን ሰው ጥርስ አውልቆ ከሆነ ከጥርሶቹ አንዱን ያውልቁት” (ፈሊጣዊ አባባል ይመልከቱ)

ማንም አንድን ሰው የሚገድል ይገደል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሰውን የሚገድለውን ሰው ይግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 24:22

ሕጉን አደረጉ

“ሕጉን ታዘዙ”


Chapter 25

1 ያህዌ በሲና ተራራ ላይ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 2 “ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ንገራቸው፣ ‹እኔ ወደሰጠኋችሁ ምድር ስትገቡ፣ ምድሪቱ ለያህዌ የሰንበት ዕረፍት ታክብር፡፡ 3 እርሻህን ለስድስት አመታት ታርሳለህ፣ ለስድስት አመታት የወይን ተክልህን እየገረዝህ ምርቱን ትሰበስባህ፡፡ 4 በሰባተኛው አመት ግን፣ ለምድሪቱ የከበረ የሰንበት ረፍት ይሁንላት፣ ለያህዌ ሰንበት ነው፡፡ እርሻህን አታርስም፡፡ ወይም የወይን ተክልህን አትገርዝም፡፡ 5 ሳትዘራው የበቀለውን አትጨደው፣ ያልገረዝከውን የወይን ተክል ፍሬ አትለቅመውም፡፡ ይህ ለምድሪቱ የከበረ የእረፍት አመት ነው፡፡ 6 ያልሰራህበት ምድር በሰባተኛው ዓመት ያፈራችው ሁሉ ለአንተ ምግብ ይሆናል፡፡ አንተ፣ ወንድና ሴት ባሮችህ፣ ለቅጥረኛ አገልጋዮችህ እና ከአንተ ጋር ለሚኖሩ መጻተኞች ምግብ ይሁን፡፡ 7 ምድሪቱ ያፈራችውን ሁሉ የቤት እንስሳትህና የዱር እንስሳት ይመገቡት፡፡ 8 ሰባት የሰንበት አመታትን ቁጠር፣ ይህም ማለት፣ ሰባት ጊዜ ሰባት አመታት ነው፣ ስለዚሀ ሰባት የሰንበት አመታት ይሆናሉ፣ ድምሩ አርባ ዘጠኝ አመታት ነው፡፡ 9 በሰባተኛው ወር በአስረኛው ቀን ከፍ ያለ የመለከት ድምጽ በሁሉም ስፍራ ንፉ፡፡ በማስተሰርያ ቀን በምድራችሁ ላይ ሁሉ መለከት ንፉ፡፡ 10 አምሳኛውን አመት ለያህዌ ለዩና በምድሪቱ ላይ ለሚኖሩ ነዋሪዎች ሁሉ ነጻነትን አውጁ፡፡ ይህ ለእናንተ ንብረትና ባሮች ወደየቤተሰቦቻቸው የሚመለሱበት ኢዩቤልዩ ይሆንላችኋል፡፡ 11 አምሳኛው አመት ለእናንተ ኢዮቤልዮ ይሆናል፡፡ አትተክሉም ወይም አዝመራ አትሰበስቡም፡፡ ሳትዘሩ የበቀለውን ብሉ፣ ሳትገርዙት ወይናችሁ ያፈራውን ፍሬ ሰብስቡ፡፡ 12 ኢዮቤልዩ ነውና፣ ለእናንተ ቅዱስ ይሆናል፡፡ በሜዳ ሳትዘሩት የበቀለውን ምርት ብሉ፡፡ 13 በዚህ የኢዮቤልዩ አመት የእያንዳንዱን ሰው ንብረት መልሱለት፡፡ 14 ለጎረቤትህ ማናቸውንም መሬት ሸጠህለት ቢሆን ወይም ከጎረቤትህ ማንኛውንም መሬት ገዝተህ ቢሆን አንዱ ሌላውን አያታል ወይም እርስ በእርሱ ያልተገባ ነገር አታድርጉ። 15 ከጎረቤትህ መሬት ብትገዛ፣ እስከ መጪው ኢዮቤልዩ ድረስ ያሉትን አመታት እና ሊሰበሰብ የሚችለውን ሰብል ከግምት አስገባ፡፡ መሬቱን የሚሸጠው ጎረቤትህም እነዚህን ነገሮች ከግምት ያስገባል፡፡ 16 እስከ መጪው ኢዮቤልዩ ለመድረስ ብዙ አመታት የሚቀር ከሆነ ይህ የመሬቱን ዋጋ ከፍ ያደርገዋል፣ እስከ መጪው ኢዮቤልዩ ለመድረስ ጥቂት አመታት የሚቀር ከሆነ ይህ የመሬቱን ዋጋ ዝቅ ያደርገዋል፣ ምክንያቱም ለአዲሱ የመሬቱ ባለቤት መሬቱ የሚሰጠው አዝመራ መጠን ለሚቀጥለው ኢዮቤልዩ ለመድረስ ከቀረው አመታት ቁጥር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ 17 አንዳችሁ ሌላችሁን አታታሉ ወይም አንዳች ሌላችሁን አታሳስቱ፤ ይልቁንም አምላካችን አክብሩ፣ እኔ አምላካች ያህዌ ነኝ፡፡ 18 ስለዚህ ትዕዛዛቴን ጠብቁ፣ ህግጋቴን ፈጽሙ እናም አድርጓቸው፡፡ ይህን ካደረጋችሁ በምድሪቱ ላይ በሰላም ትቀመጣላችሁ፡፡ 19 ምድሪቱ ምርቷን ትሰጣለች፣ እናንተም ትጠግባላችሁ በዚያም በሰላም ትኖራላችሁ፡፡ 20 እንዲህ ልትሉ ትችላላችሁ “በሰባተኛው አመት ምን እንበላለን አንዘራም፣ ምርታችንንም አንሰበስብምና፡፡” 21 በስድስተኛው አመት በረከቴ እንዲሆንላችሁ በእናንተ ላይ አዛለሁ፣ ምድሪቱ ለሶስት አመታት የሚሆን ምርት ትሰጣለች፡፡ 22 በስምንተኛው አመት ትተክላላችሁ፣ በቀደሙት አመታት ካመረታችሁትና ከሰበሰባችሁት ምግብ መብላት ትቀጥላላችሁ፡፡ 23 መሬት ለአዲስ ጊዜያዊ ባለቤቶች አይሸጥ፣ ምክንያቱም መሬቷ የእኔ ናት፡፡ እናንተ ሁላችሁም በምድሬ ላይ እንግዶችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች ናችሁ፡፡ 24 የያዛችሁትን ምድር ሁሉ የመቤዠት መብት እንዳላችሁ ማስተዋል አለባችሁ፤ በገዛችሁት ቤተሰብ መሬቱ ተመልሶ እንዲገዛ መፍቀድ አለባችሁ፡፡ 25 እስራኤላዊ ወገናችሁ ደሃ ቢሆንና በዚህም ምክንያት ከንብረቱ ቢሸጥ፣ የቅርብ ዘመዱ ለአንተ የሸጠልህን ንብረት መልሶ ይግዛ፡፡ 26 ሰውዬው ንብረቱን የሚቤዥለት ምንም ዘመድ ባይኖረው፣ ነገር ግን ሀብት ቢያፈራና ንብረቱን መልሶ መቤዠት ቢችል፣ 27 መሬቱ ከተሸጠበት ጊዜ አንስቶ ያሉትን አመታት ያሰላና ለሸጠለት ሰው ቀሪ ሂሳቡን ይክፈል፡፡ ከዚያ ወደ ራሱ ንብረት ይመለስ፡፡ 28 ነገር ግን መሬቱን ለራሱ ማስመለስ ባይችል፣ የሸጠው መሬት እስከ ኢዮቤልዩ አመት ድረስ በገዛው ሰው ባለቤትነት ስር ይቆያል፡፡ በኢዮቤልዩ አመት፣ መሬቱ ለሸጠው ሰው ይመለስለታል፣ ከመሰረቱ ባለቤት የነበረው ወደ ንብረቱ ይመለሳል፡፡ 29 አንድ ሰው በተቀጠረ ከተማ ውስጥ የሚገኝ ቤቱን ቢሸጥ፣ በተሸጠበት በአመት ጊዜ ውስጥ መልሶ ሊገዛው ይችላል፡፡ 30 ለአንድ ሙሉ አመት ውስጥ ካልተቤዠ፣ በተቀጠረ ከተማ ውስጥ የሚገኘው ቤት፣ የገዛው ሰው ትውልድ የልጅ ልጅ ቋሚ ንብረት ይሆናል፡፡ ያ ቤት በኢዮቤልዩ ተመላሽ አይሆንም፡፡ 31 ነገር ግን በዙሪያቸው ቅጥር የሌላቸው መንደሮች ቤቶች ከአገሩ የእርሻ መሬት ጋር የሚታዩ ንብረቶች ይሆናሉ፡፡ ተመልሰው ሊዋጁ ይችላሉ፣ በኢዮቤልዩ ተመላሽ ይሆናሉ፡፡ 32 ሆኖም፣ የሌዋውያን ንብረት የሆኑ ቤቶች በማንኛውም ጊዜ ሊዋጁ ይችላሉ፡፡ 33 ከሌዋዊያን አንዱ የሸጠውን ቤት መልሶ ባይቤዥ፣ በከተማ ውስጥ የሚኘው የተሸጠው ቤት በኢዮቤልዩ ተመላሽ ይሆናል፣ በከተማ የሚገኝ የሌዋዊ ቤቶች በእስራኤል ሰዎች መሀል የእነርሱ ንብረት ነው፡፡ 34 በከተማዎቻቸው ዙሪያ የሚገኙ እርሻዎች ግን አይሸጡም ምክንያቱም እነዚህ የሌዋዊያን ቋሚ ንብረት ናቸው፡፡ 35 የአገራቸው ሰው ወገናችሁ ደሃ ቢሆን፣ ስለዚህም ራሱን መቻል ቢያቅተው፣ መጻተኛውን እንደምትረዱ እርዱት ወይም በመሀከላችሁ የሚኖርን ባዕድ እንደምትረዱ ዕርዱት፡፡ 36 ወለድ አታስከፍሉት ወይም በማናቸውም መንገድ ከእርሱ ትርፍ ለማግኘት አትሞክሩ፣ ነገር ግን እግዚአብሔርን አክብሩ በመሆኑም ወንድማችሁ ከእናንተ ጋር አብሮ መኖር ይችላል፡፡ 37 በወለድ ገንዘብ አታበድሩት፣ ወለድም አታስከፍሉት፣ ትርፍ ለማግኘት ምግባችሁን አትሽጡለት፡፡ 38 የከነዓንን ምድር እሰጣችሁና አምላካችሁ እሆን ዘንድ ከግብጽ ምድር ያወጣኋችሁ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ 39 የአገርህ ሰው ወገንህ ደሃ ቢሆንና ራሱን ለአንተ ቢሸጥ፣ እንደ ባሪያ አታሰራው፡፡ 40 እንደ ተቀጣሪ አገልጋይ አስተናግደው፡፡ ከአንተ ጋር በጊዜያዊነት እንደሚኖር ሰው ይሁን፡፡ እስከ ኢዮቤልዩ አመት ድረስ በአንተ ዘንድ ያገለግል፡፡ 41 ከዚያ ከአንተ ዘንድ ይሄዳል፣ እርሱና ከእርሱ ጋር ያሉ ልጆቹ፣ ወደ ራሱ ቤተሰቦችና ወደ አባቱ ይዞታ ይመለሳሉ፡፡ 42 እነርሱ ከግብፅ ምድር ያወጣኋቸው አገልጋዮቼ ናቸውና፡፤ እንደ ባሪያዎች አይሸጡም፡፡ 43 በጭካኔ ልትገዛቸው አይገባም፣ ነገር ግን አምላክህን አክብር፡፡ 44 በዙሪያህ ከሚኖሩ ህዝቦች ወንድና ሴት ባሪያዎችን ከእነርሱ መሀል መግዛት ትችላለህ፡፡ 45 በመሀልህ ከሚኖሩ መጻተኞችም ባሪያዎችን መግዛት ትችላለህ፣ ይህም ማለት፣ ከአንተ ጋር ካሉ ቤተሰቦቻቸው፣ በምድርህ ከተወለዱ ልጆች ባሪያዎችን መግዛት ትችላለህ፡፡ እነርሱ የአንተ ሀብት ይሆናሉ፡፡ 46 እንዲህ ያሉትን ባሪያዎች ንብረት አድርገው እንዳይዟቸው ከአንተ በኋላ ለልጆችህ ውርስ አድርገህ መስጠት ትችላለህ፡፡ ከእነርሱ ሁልጊዜም ባሪያዎችህን መግዛት ትችላለህ ነገር ግን ከእስራኤላዊያን መሀል በወንድሞችህ ላይ በጭካኔ መግዛት የለብህም፡፡ 47 መጻተኛው ወይም ከአንተ ጋር በጊዜያዊነት ከሚኖረው እንግዳ መሃል አንዱ ባለጸጋ ቢሆንና ከእስራኤላዊ ወገንህ መሃል አንዱ ደሃ ቢሆን፣ ለራሱም ለዚያ ባዕድ ቢሸጥ፣ ወይም ከባዕዳን ቤተሰብ መሃል ለአንዱ ቢሸት፣ 48 እስራኤላዊ ወገንህ ከተገዛ በኋላ ተመልሶ ይገዛ፡፡ ከቤተሰቡ መሃል አንዱ ይቤዠው፡፡ 49 የሚቤዠው አጎቱ፣ የአጎቱ ልጅ፣ ሊሆን ይችላል፣ ወይም ከቤተሰቡ ውስጥ ማንኛውም የቅርብ ዘመዱ ሊቤዠው ይችላል፡፡ ወይም፣ እርሱ ራሱ ባለፀጋ ቢሆን፣ ራሱን መቤዠት ይችላል፡፡ 50 ከገዛው ሰው ጋር ይደራደር፣ ለገዛው ሰው ራሱን ከሸጠበት አመት ጀምረው እስከ ኢዮቤልዩ አመት ድረስ ይቁጠሩ፡፡ የመቤዣው ዋጋ ለገዛው ሰው መስራቱን መቀጠል በሚኖርበት አመታት ቁጥር ለተቀጣሪ አገልጋይ በሚከፍለው ክፍያ ይሰላል፡፡ 51 እስከ ኢዮቤልዩ ለመድረስ ብዙ አመታት የሚኖር ከሆነ፣ ለቤዣው መልሶ የሚከፍለው የገንዘብ መጠን ከእነዚያ ቀሪ አመታት ጋር የተመጣጠነ ይሁን፡፡ 52 ለኢዮቤልዩ አመት የቀሩት አመታት ጥቂት ከሆኑ፣ ከገዛው ሰው ጋር ለኢዮቤልዩ በቀሩት አመታት ልክ ይደራደር፣ ለመቤዣው በቀሩት አመታት ውስጥ ይክፈለው፡፡ 53 በየዓመቱ እንደ ቅጥር ሰው ይኑር፡፡ በግፍ አለመስተናገዱን ማረጋገጥ ይገባሃል፡፡ 54 በእነዚህ መንገዶች ካልተዋጀ፣ እስከ ኢዮቤልዩ አመት ድረስ እርሱና ከእርሱ ጋር ልጆቹም አብረው ያገልግሉ፡፡ 55 እስራኤላውያን የእኔ አገልጋዮቼ ናቸው፡፡ ከግብጽ ምድር ያወጣኋቸው አገልጋዮቼ ናቸው፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡”



Leviticus 25:1

ምድሪቱ ራሰዋ የእግዚአብሔርን ሰንበት ታብር

ምድር በሰንበት ማረፍን እንደሚታዘዝ ሰው ተደርጋ ተገልጻለች ሰዎች በየስንበቱ እንደሚያርፉ ሁሉ በሰባተኛው ዓመት ምድሪቱ ን ባለማረስ ሰዎች እግዚአብሔርን ያከብራሉ:: አት: “ምድሪቱ በሰባተኛው ቀን ለእግዚአብሔር እንዲትርፍ የሰንበትን ሕግ ጠብቁ” ወይም “በሰባተኛው ዓመት ምድሪቱን ባለማረስ የእግዚአብሔርን ሰንበት ጠበቁ” (ሰውኛ አገላለጽና ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 25:3

ወይንህን ግረዝ

ወይንን መገረዝ ጥሩ ፍሬ እንዲያፈራ የወይኑን ተክልና ቅርንጫፎቹን መቁረጥ ማለት ነው ፡፡

ምድሪቱ የዕረፍት ሰንበት ታክብር ምድሪቱን አለማረስ ምድሪቱን እንደማሳረፍ ተነግሮአል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የምድሪቱን የዕረፍት ሰንበት አክብሩ” ወይም “ምድሪቱን በሰባተኛው ዓመት ባለማረስ የሰንበትን ሕግ ጠብቁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:5

አትሰብስብ….ከአንተ ጋር ለሚኖር ምግብ ይሁን

25: 5-6 እንደሚናገረው የእርሻው ባለቤት እንደመጀመሪያዎቹ ስድስት ዓመታት ሠራተኞችንና ምርቱን መቆጣጠር እግዚአብሔር አይፈቅድም ነገር ግን ግለሰቦች ወደ እርሻዎች በመውጣት ያገኙትን ፍሬ እንዲለቅሙና እንዲበሉ ይፈቅዳል፡፡

ያልተገረዘው የወይን ተክል

ለስድስት ዓመታት እንደሚየደርጉት ማንም ያልተንከባከውን ወይም ያልገረዘውን ወይን ማለት ነው ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ያልገረዙአቸው ወይኖቻችሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ማንኛውም ያልተሠራ እርሻ ያበቀለው

ባልተሠራ መሬት የሚበቅለው ማንኛውም

ያልተሠራ መሬት በስድስ ዓመታት እንደሚያደርጉት ማንም ያልተንከባከበው ማሣ ወይም እርሻ ማለት ነው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ያላረሳችሁት ማሣዎቻችሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ምድሪቱ የሚታስገኘው ማንኛውም

በምድሪቱ የሚበቅለው ማንኛውም

Leviticus 25:8

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ መናገር ይቀጥላል

ሰባት የሰንበት ዓመታት ይሆናሉ

“ሰባት ምድብ ሰባት ዓመታት”

ዐርባ ዘጠኝ ዓመታት

“49 ዓመታት” (ቁጥሮች ይመልከቱ)

የሰባተኛው ወር አሥረኛው ቀን

በዕብራይስጥ የቀን መቁጠሪያ ሰባተኛ ወር ነው:: በምዕራባዊያን አቆጣጠር አሥሪኛው ቀን መስከረም ወር መጨረሻ አካባቢ ነው:: (የዕብራዊያን ወራትና መደበኛ ቁጥሮች ይመልከቱ)

የሥርየት ቀን

የእስራኤልን ሕዝብ ኃጢአት ሁሉ እግዚአብሔር ይቅር እንዲል በየዓመቱ በዚህ ቀን ሊቀካህኑ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት ያቀርባል በዘሌዋዊያን 23:27 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

Leviticus 25:10

ሃምሳኛ ዓመት

ይህ መደበኛ ቁጥር ነው፡፡ አት፡ 5ዐ ዓመት (ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ኢዩቤልዩ ይሁንላችሁ

ኢዩቤልዩ መሬትን ለርስቱ ባለቤት የሚመልሱበትና ለባሪያዎች ነጻነትን የሚያወጁበት ዓመት ነው አት: “ምርኮ የመመለስ ዓመት” ወይም “መሬት የመመለስና ለባሪያዎች የነጻነት ዓመት”

ንብረትና ባሪያዎች ይመለሳሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ንብረትንና ባሪያዎችን መልሱ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:11

ኢዩቤልዩ ይሁንላችሁ

“የምርኮ ዓመት” ወይም “መሬትን የመመለስ ዓመት” ለማን መሬትን እንደሚመልሱ ግልጽ ተደረግ አለበት:: አት: “ለእኔ መሬትን የሚትመልሱበት ዓመት” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ሳትዘሩ በሜዳ የበቀለውን ብሉ

የእርሻው ባለቤት እንደመጀመሪያዎቹ ስድስት ዓመታት ሠራተኞችንና ምርቱን መቆጣጠር እግዚአብሔር አልፈቀደም:: ነገር ግን ግለሰቦች ወደ እርሻዎች በመውጣት ያገኙትን ፍሬ እንዲለቅሙና እንዲበሉ ፈቅዶአል፡፡

Leviticus 25:13

በዚህ በኢዩቤልዩ ዓመት

“በዚህ የመመለስ ዓመት” ወይም “በዚህ የመሬት መመለስና የባሪያ ነጻ መውጣት ዓመት”

Leviticus 25:15

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ በናገሩን ቀጠለ

ሊሰበሰብ ይችላል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሊትሰበሰቡ ትችላላችሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የሚቀጥለው ኢዩቤልዩ

x

Leviticus 25:18

ሥርዓቴን ጠብቁ ሕጌን ታዘዙ እናም አድርጉት

እነዚህ ሀረጐች ሁሉ በመሠረቱ ተመሣሣይ ትርጉም አላቸው:: እግዚአብሔር የተናገረውን ማንኛውንም ነገር ሕዝብ እንዲታዘዝ ትኩረት ይሰጣሉ (ተመሣሣይ ተጓዳኝ ንጽጽር ይመለከቱ)

እስኪትጠግቡ ትበላላችሁ

ሆዳችሁ እስኪጠግብ በቂ ምግብ ትበላላችሁ:: አት: “እስኪትጠግቡ ትበላላችሁ” ወይም “ብዙ ምግብ ትበላላችሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:20

እናንተም ትላላችሁ

እዚህ እናንተ የእስራኤልን ሕዝብ ያመለክታል (ሁለተኛ ሰው አገላለጽ ይመልከቱ)

በረከተን እሰድድላችኋለሁ

እግዚአብሔር እንደሚታዘዝለት ሰው አድርጐ ስለ በረከቱ ይናገራል፡፡ አት፡ “በረከተን እልክላችኋለሁ ወይም እባርካችኋለሁ” (ሰውኛ አገላለጽ ይመልከቱ)

ቀድሞ ከሰበሰባችሁት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ከሰበሰባችሁት ምግብ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:23

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር መናገሩን ይቀጥላል

መሬት ለዘለቄታው አይሸጥ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “መሬትን ለዘለቄታው ለአንድ ሰው አትሽጡ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

መሬት የሚዋጅበት እንዲኖር አድርጉ

መዋጀት የሚለው ስም “ሊዋጅ” ወይም “እንደገና ሊገዛ” በሚሉ ግሶች ሊገለጽ ይችላል:: አት: “የመሬቱ ባለቤት መሬቱን በፈለገበት ጊዜ መዋጀት እንደሚችል ይታወቅ” (ረቂቅ ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

የቅርብ ዘመዱ መጥቶ ወገኑ የሸጠውን ይዋጅለት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የቅርብ ዘመዱ ወገኑ የሸጠውን እንዲዋጅለት አድርጉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:26

መሬት ከተሸጠ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “መሬቱን ከሸጠ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የዋጋውን ልዩነት ለገዛው ሰው ይመልስ

ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት: “ገዢው የገዛውን ገንዘብ መጠን ይመልስልት” (ግምታም እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የኢዩቤልዩ ዓመት

የመመለስ ዓመት መሬት የሚመለስበት ዓመት በዘሌዋዊያን 25: 1ዐ ይህን እንዴት እንተረጐሙ ይመልከቱ::

መሬት ይመለሳል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የገዛ ሰው መሬቱን ይመልሳል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ወደ ርስቱ ይመለሳል

ወደ ራሱ መሬት ይመለሳል

Leviticus 25:29

ከተሸጠ በኋላ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እርሱ ከሸጠ በኋላ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የመዋጀት መብት

“መዋጀት” የሚለው ስም “ሊዋጅ” ወይም “እንደገና ሊገዛ” በሚሉ ግሶች ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ሊዋጅ መብት አለው” (ረቂቅ ስሞችን ስለመተርጐም ይመልከቱ)

ቤቱ ካልተዋጀ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እርሱ ወይም ቤተሰቡ/ወገኑ ቤቱን ካልዋጀው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አይወለስለትም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “የገዛው ሰው ቤቱን አይመልስለትም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የኢዩቤልዩ ዓመት

“የመመለስ ዓመት” ወይም “መሬት የሚመለስበትና ባሪያዎች ነጻ የሚወጡበት ዓመት”

Leviticus 25:31

ቅጥር በዙሪያው ባልተሠራለት መንደር

አንዳንድ መንደሮች በዙሪያቸው ቅጥር የላቸውም

ሊዋጁና ሊመለሱ ይችላሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እነዚያን ቤቶች መዋጀት ይችላሉ እናም የገዙአቸውም ይመልሱ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የኢዩቤልዩ ዓመት

“የመመለስ ዓመት” ወይም “መሬት የሚመለስበትና ባሪያዎች ነጻ የሚወጡበት ዓመት”

ሌዋዊያን የራሳቸው በሆኑት ከተሞች ውጥ የሚገኙትን ቤቶቻቸውን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሌዋዊያን በከተሞቻቸው ያሉ ቤቶቻቸውን” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ምን ጊዜም ሊዋጁ ይችላሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ሌዋዊያን እነዚያን ምን ጊዜም ሊዋጁ ይችላሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:33

በከተማው ውስጥ የሚገኘው የተሸጠው ቤት ይመለሳል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “በከተማው ውስጥ ያለውን ቤት የገዛ ይመልሳል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:35

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ አንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ወለድ አትቀበለው

ካበደርከው ተጨማሪ እንዲከፍል አታድርግ

Leviticus 25:39

እንደባሪያ አድርገህ አታስሠራው እንደ ቅጥር ሠራተኛ ቁጠረው

ባለቤቱ እስራኤላዊውን ባሪያ ሳይሆን እንደ ተከበረ ሰው ይቁጠረው ማለት ነው::

የኢዩቤልዩ ዓመት ነው

“የመመለስ ዓመት” ወይም “መሬት የሚመለስበትና ባሪያዎች ነጻ የሚወጡበት ዓመት”

Leviticus 25:42

አገናኝ ዐረፍተ ነገር

ለሕዝቡ ምን መናገር እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

አገልጋዮቼ ናቸው

የአገረው ሰዎች አገልጋዮቼ ናቸው

እንደባሪያዎች አይሸጡ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እንደ ባሪያዎች አትሽጡአቸው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ከእነዚያ ባሪያዎችን ግዙ

“ከአሕዛብ መካከል ባሪያዎችን ግዙ”

Leviticus 25:47

አንድ እስራኤላዊ ወገን ቢሽጥ ከተሸጠ በኋላ ሊዋጅ ይችላል፤ ከዘመዶቹ አንድ ይዋጀው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “መጻተኛ የእስራኤላዊውን ወገን ከገዛ በኋላ ከእስራኤላዊ ቤተሰብ አንድ ሰው ይህን ሰው ይዋጀው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 25:49

እስከ ኢዩበልዩ ዓመት

እስራኤላዊ ባሪያ ሊሆን የሚችለው እስከ ኢዩቤልዩ ዓመት ብቻ ነው እነዚህ መመሪያዎች ቢሆኑም ከኢዩቤልዩ ዓመት በፊት ነጻነቱን ሊዋጅ ቢፈልግ ይችላል::

የኢዩቤልዩ ዓመት

“የመመለስ ዓመት” ወይም “መሬት የሚመለስበትና ባሪያዎች ነጻ የሚወጡበት ዓመት”

የመዋጀት ዋጋው ይተመናል

ይተመናል የሚለው ግሥ በተሻጋሪ ግሥ ሊገለጽ ይችላል አት፤ “የመዋጀቱን ወጋ ይተምናሉ ” ወይም እስራኤላዊውን ነጻ ለማውጣት ለመጻተኛው ምን ያህል መከፈል እንዳለበት ይተምናሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ለአንድ ቅጥር ሠራተኛ በሚከፈለው መሠረት

እስራኤላዊው ነጻነቱን ከተዋጀ እስራኤላዊው መሥራት የሚገባው ነገርግን ያልሠራውን ለማሥሠራት መጻተኛው አገልጋይ መቅጠር ይኖርበታል:: “ተከፈለ” እናም “ተቀጠረ” የሚሉ ግሶች በተሻጋሪ ግሥ መልክ ሊገለጹ ይችላሉ:: አት፤ “ለአንድ ቅጥር ሠራተኛ በሚከፈለው ተመን መሠረት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በቀጣይ መሥራት የነበረባቸውን ዓመታት

“እስራኤላዊው መሥራት የሚገባቸው ነገርግን ያማይሠራባቸው እስከ ቀጣይ ኢዩቤልዩ ያሉ ዓመታት ቁጥር”

Leviticus 25:51

ይክፈል

እስራኤላዊው በሪያ ይክፈል

Leviticus 25:53

እንክብካቤ ይደረግለት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “እንደባሪያ አድርጐ የገዛው መጻተኛ ይንከባከበው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በጭካኔ አይግዛ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: አት፤ “ማንም አይጨክንበት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በእነዚህ መንገዶች ካልተዋጀ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: እናም የሚዋጀው ሰው ግልጽ ሊደረግ ይችላል:: አት፤ “ባሪያ አድርጐ ከገዛው ማንም በእነዚህ መንገዶች የማይዋጀው ከሆነ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር እና ግምታዊ እውቀትና ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በእነዚህ መንገዶች

በዚህ መንገድ

እስከ ኢዩቤልዩ ዓመት እርሱና ልጆቹ ያገልግሉ

እስራኤላዊው ባሪያና ልጆቹ እስከ ኢዩቤልዩ ዓመት መጻተኛውን ያገልግሉ እናም ከዚያ በኋላ መጻተኛው እስራኤላዊውንና ልጀቹን ነጻ ይልቀቅ

እስራኤላዊያን ለእኔ አገልገዮቼ ናቸው

እስራኤላዊያን አገልጋዮቼ ናቸው


Chapter 26

1 “እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፤ ጣኦታትን አታብጁ፣ የተቀረጸ ምስልንም አታቁሙ፣ ወይም ለአምልኮ የድንጋይ አምዶችን አታቁሙ፣ እንደዚሁም ልትሰግዱላቸው ማናቸውንም የቀረፀ የድንጋይ ምስል በምድራችሁ አታድርጉ፡፡ 2 ሰንበቴን ጠብቁ የተቀደሰውን ስፍራዬን አክብሩ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 3 በህጌ ብትኖሩና ትዕዛዛቴን ብትጠብቁ ብትታዘዟቸውም፣ 4 ዝናብን በወቅቱ እሰጣችኋለሁ፤ ምድር ምርቷን ትሰጣችኋለች፣ የሜዳ ዛፎችም ፍሬያቸውን ይሰጧችኋል፡፡ 5 የወቃችሁት እስከ ወይን አዝመራችሁ ድረስ ይቆያል፣ የወይን ፍሬ አዝመራችሁም እስከምትዘሩበት ወቅት ድረስ ይቆያል፡፡ እንጀራችሁን በምድሪቱ ቤታችን በሰራችሁበት ጠግባችሁ ትበላላችሁ በእረፍት ትኖራላችሁ፡፡ 6 በምድሪቱ ሰላምን እሰጣለሁ፣ ምንም ነገር ሳያስፈራችሁ ተዘልላችሁ ትቀመጣላችሁ፡፡ ከምድሪቱ አደገኛ እንስሳትን አስወጣለሁ፣ በምድራች ሰይፍ አያልፍም፡፡ 7 ጠላቶቻችሁን ታሳድዳላችሁ፣ እነርሱም በፊታችሁ በሰይፍ ይወድቃሉ፡፡ 8 ከእናንተ አምስታችሁ መቶውን ታሳድዳላችሁ፣ ከእናንተ መቶው አስር ሺኅ ያሳድዳል፤ ጠላቶቻች በፊታችሁ በሰይፍ ይወድቃሉ፡፡ 9 ወደ እናንተ በሞገስ እመለከታለሁ፣ ፍሬያማም አደርጋችኋለሁ፣ አበዛችሁማለሁ፤ ከእናንተ ጋር ቃል ኪዳኔን አደርጋለሁ፡፡ 10 ለረጅም ጊዜ የተከማቸ እህል ትበላላችሁ፡፡ ለአዲሱ ምርታችሁ ስፍራ ስለሚያስፈልጋችሁ የተከማቸውን እህል ታወጣላችሁ፡፡ 11 ማደሪያዬን በመካከላችሁ አደርጋለሁ፣ እኔም እናንተን አልጣላችሁም፡፡ 12 በመካከላችሁ እሆናለሁ አምላካችሁም እሆናለሁ፣ እናንተም የእኔ ህዝብ ትሆናላችሁ፡፡ 13 ከግብጽ ምድር ያወጣኋቸው፣ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፣ ስለዚህም የእነርሱ ባሮች አትሆኑም፡፡ የቀንበራችሁን ብረት ሰብሬያሁ፣ ቀና ብላችሁ እንድትሄዱ አድርጌያለሁ፡፡ 14 ነገር ግን እኔን ባትሰሙኝ፣ እነዚህን ትዕዛዛቴን ሁሉ ባትጠብቁ፣ 15 ትዕዛዛቴን ብትተዉና ህግጋቴን ብትጠሉ፣ እናም ትዕዛዞቼን ሁሉ ሳትፈጽሙ ብትቀሩ፣ ነገር ግን ቃልኪዳኔን ብታፈርሱ 16 እነዚህን ነገሮች ብታደርጉ፣ እኔም ይህን አደርግባችኋለሁ፡ ፍርሃትን እሰድባችኋለሁ፣ ዐይኖችንና ሕይወታችሁን የሚያጠፋ በሽታና ትሳት አደርስባችኋለሁ፡፡ በከንቱ ትዘራላችሁ፣ ምክንያቱም ፍሬያቸውን ጠላቶቻችሁ ይበሉታል፡፡ 17 ፊቴን በጠላትነት ወደ እናንተ እመልሳለሁ፣ ከጠላቶቻችሁ ሀይል በታች ትወድቃላችሁ፡፡ የሚጠሏችሁ ሰዎች ይገዙዋችኋል፣ ማንም ሳያሳድዳችሁ እንኳን ትሸሻላችሁ፡፡ 18 ትዕዛዛቴን ባትሰሙ፣ ከዚህ በኋላ ስለ ሀጢአታችሁ ሰባት እጥፍ እቀጣችኋለሁ፡፡ 19 የትእቢታችሁን ኃይል እሰብራለሁ፡፡ ሰማይን በላያችሁ እንደ ብረት ምድራችሁንም እንደ ናስ አደርጋለሁ፡፡ 20 ብርታታችሁ ለአንዳች ነገር አይጠቅምም፣ ምክንያቱም ምድራችሁ አዝመራዋን አትሰጥም፣ በምድራችሁ ዛፎቻችሁ ፍሬያቸውን አይሰጡም፡፡ 21 በእኔ ላይ ጠላት ሆናችሁ ብትመላለሱና ከኃጢአታችሁ በላይ እኔን ባትሰሙኝ፣ በእናንተ ላይ ሰባት ዕጥፍ ድንጋጤ አመጣለሁ፡፡ 22 ልጆቻችን የሚነጥቁ፣ ከብቶቻችሁን የሚያጠፉ፣ እናንተን በቁጥር ጥቂት የሚያደርጉ አደገኛ አውሬዎችን እሰድባችኋሉሁ፡፡ ስለዚህም ጎዳናዎቻችሁ በረሃ ይሆናሉ፡፡ 23 በእነዚህ ሁሉ ነገሮች ትምህርቶቼን ባትሰሙ ነገር ግን በእኔ ላይ ጠላት ሆናችሁ መመላለሳችሁን ብትቀጥሉ፣ 24 እኔም በእናንተ ላይ ጠላት እሆናለሁ፡፡ እኔ ራሴ በሀጢአቶቻችሁ ሰባት እጥፍ እቀጣችኋለሁ፡፡ 25 ቃልኪዳን በማፍረሳችሁ በእናንተ ላይ የበቀል ሰይፍ አመጣለሁ፡፡ በከተሞቻችሁ ውስጥ በአንድነት ትሰበሰባላችሁ፣ በዚያም በማህላችሁ በሽታን እልካለሁ፣ እናንተም በጠላቶቻችሁ ሀይል ትሸነፋላችሁ፡፡ 26 የምግብ አቅርቦታችሁን ስቆርጥ፣ አስር ሴቶች በአንድ ምድጃ እንጀራችሁን ይጋግራሉ፣ እንጀራችሁንም በሚዛን ያካፍሏችኋል፡፡ ትበላላችሁ ነገር ግን አትጠግቡም፡፡ 27 እነዚህ ነገሮች ሁሉ ሆነው ባትሰሙት፣ ነገር ግን በእኔ ላይ በጠላትነት መመላሳችሁን ብትቀጥሉ፣ 28 እኔ በቁጣ እመጣባችኋለሁ፣ በኃጢአቶቻችሁ ሰባት እጥፍ እቀጣችኋለሁ፡፡ 29 ወንድ ልጆቻችሁን ስጋና የሴት ልጆቻችሁን ስጋ ትበላላችሁ፡፡ 30 የአምልኮ ሥፍራችሁን አጠፋለሁ፣ የእጣን መሰዊያዎቻችሁን እቆርጣለሁ፣ በድኖቻችሁን በድን በሆኑ በጣኦቶቻችሁ ላይ እጥላለሁ፣ ደግሞም እኔ ራሴ እጸየፋችኋለሁ፡፡ 31 ከተሞቻችሁን ፍርስራሽ አደርጋለሁ የተቀደሱ ቦታዎቻችሁን አጠፋለሁ፡፡ በመስዋዕቶቻችሁ መዓዛ ደስ አልሰንም፡፡ 32 ምድሪቱን አጠፋለሁ፡፡ በዚያ የሚኖሩ ጠላቶቻችሁ በጥፋቱ ይደነግጣሉ፡፡ 33 በአገራት መሃል እበትናችኋለሁ፣ ሰይፌን መዝዤ አሳድዳችኋለሁ፡፡ ምድራችሁ ባድማ ትሆናለች፣ ከተሞቻችሁም ፍርስራሽ ይሆናሉ፡፡ 34 ከዚያም ምድሪቱ ባድማ ሆኖ እስከቆየች ድረስና እናንተ በጠላቶቻችሁ ምድር እስከቆያችሁ ድረስ የሰንበት ዕረፍቷን ታገኛለች፡፡ በነዚያ ጊዜያት፣ ምድሪቱ ታርፋለች ሰንበቶቿንም ታገኛለች፡፡ 35 ፍርስራሽ ሆና እስከቆየች ድረስስ እረፍት ይሆንላታል፣ እናንተ በውስጧ ስትኖሩ በሰንበቶቻችሁ ያላገኘችውን ዕረፍት ታገኛች፡፡ 36 እናንተ በጠላቶቻችሁ ምድር በቀራችሁት ላይ በልቦቻችሁ ውስጥ ፍርሃት እሰዳለሁ፣ ስለዚህም የቅጠል ኮሰሽታ እንኳን ያስደነግጣችኋል፣ ከሰይፍ እንደሚሸሽ ትሆናላች፡፡ ማንም ሳያሳድዳችሁ ትወድቃላች፡፡ 37 ማንም ባያሳድዳችሁም እንኳን ከሰይፍ እንደሚሸሽ ሰው አንዳችሁ በሌላችሁ ላይ ትደነቃቀፋላችሁ፡፡ በጠላቶቻችሁ ፊት ለመቆም ምንም ሀይል አይኖራችሁም፡፡ 38 ከአገራት መሀል ተለይታችሁ ትጠፋላችሁ፣ የጠላቶቻችሁ ምድር ራሱ በፍርሃት ይሞላችኋል፡፡ 39 ከእናንተ መሃል የቀሩት በዚያ በጠላቶቻችሁ ምድር በሀጢአቶቻቸው ይጠፋሉ፣ እንዲሁም በአባቶቻቸው ሀጢአቶች ምክንያት ይጠፋሉ፡፡ 40 ሆኖም የእነርሱንና የአባቶቻቸውን ሀጢአቶች ቢናዘዙ፣ ለእኔ ታማኝ ካልሆኑበት ክህደታቸው ቢመለሱ፣ ከእኔ ጋር ተላት ከሆኑበት አካሄዳቸው ቢመለሱ 41 እኔ በእነርሱ ላይ እንድነሳ ካደረገንና ለጠላቶቸው ምድር አሳልፌ እንድሰጣቸው ካደረገ አካሄዳቸው ቢመለሱ ያልተገረዙ ልቦቻቸው ዝቅ ቢሉ፣ እናም በሀጢአቶቻቸው የደረሰባቸውን ቅጣታቸውን ቢቀበሉ፣ 42 ከያዕቆብ ጋር የገባሁትን ኪዳኔን አስባለሁ፤ እንዲሁም፣ ምድሪቱን አስባለሁ፡፡ 43 ምድሪቱ ለቀዋት ስለሄዱ ባዶ ትቀራለች፣ ስለዚህ ካለእነርሱ በተተወችበት ጊዜ በሰንበቶቿ ታርፋለች፡፡ እነርሱ በሀጢአታቸው ቅጣታቸውን ይቀበላሉ ምክንያቱም እነርሱ ራሳቸው ስርአቴን ትተዋል ህግጋቴንም ጠልተዋል፡፡ 44 ሆኖም ከዚህ ሁሉ ባሻገር፣ በጠላቶቸው ምድር ውስጥ ሲሆኑ፣ እኔ አልተዋቸውም ሙሉ በሙሉ እስካጠፋቸውም ድረስ አልጠላቸውም፣ ደግሞም ከእነርሱ ጋር የገባሁትን ኪዳኔን አልረሳም፣ እኔ አምላካቸው ነኝ፡፡ 45 ነገር ግን ስለ እነርሱ ስል አምላካቸው እሆን ዘንድ አሕዛብ እያዩ ከግብጽ ምድር ካወጣኋቸው ከአባቶቻቸው ጋር የገባሁትን ኪዳኔን አስባሁ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡” 46 በሙሴ በኩል ያህዌ በሲና ተራራ ላይ በራሱና በእስራኤል ህዝብ መሃል ያደረጋቸው ትዕዛዛት፣ ደንቦችና ህጎች እነዚህ ናቸው፡፡



Leviticus 26:1

X

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ሰንቤታቴን ጠብቁ

የሰንቤታቴን ሕጐች ታዘዙ

Leviticus 26:3

በሥርዓቴ ብትሄዱ ትዕዛዜን ቢትጠብቁና ብትታዘዙ

ይህም አንድ አባባል በሶስት መንገዶች መግለጽ ነው እግዚአብሔር እንዲያደርጉ ያዘዙአቸውን ማንኛውም ነገር ሕዝቡ እንዲታዘዝ ትኩረት የሚሰጡ ናቸው:: አት ትዕዛዜንና ሥርዓተን በጥንቃቄ ብትጠብቁ (ተመሣሣይ ተጓዳኝ ንጽጽር ይመልከቱ)

በሥርዓቴ ቢትሄዱ

እንደሥርዓቱ መኖር በሥርዓቱ እንደመሄድ ተደርጐ ተነግሮአል አት በሥርዓቴ መሠረት ቢትመላለሱ ወይም በሥርዓቴ መሠረት ቢትኖሩ (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 26:5

ምግባችሁን እስኪትጠግቡ ትበላላችሁ

ምግብ የተባለው ሁሉን ምግብ ዓይነት ነው እስክትጠግቡ ሆዳችሁ እስክጠግብ ማለት ነው:: አት: እስክትጠግቡ ትበላላችሁ ወይም ብዙ ምግብ ትበላላችሁ (ፈሊጣዊ አነጋገርና Synecdoche/ ክፍል ሙሉውን ሙሉው ክፍልን እንደሚወክል የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

በምድሪቱ ላይ ሰላምን እሰጣለሁ

በምድሪቱ ላይ ሰላም እንዲሆን ምክንያት አደርጋለሁ

ሰይፍም በምድራችሁ ላይ አያልፍም

እዚህ “ሰይፍ” የሚለው ቃል “የጠላት ሠራዊት” ወይም “የጠላት ጥቃት” ይወክላል:: አት “ምንም ሠራዊት አያጠቃህም” (See Metonymy/ ተዛማጅ ባሕሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላት ወይም አባባሎች ይመልከቱ)

Leviticus 26:9

ፊተን እመልሳለሁ

“መልካምነቴን አሳያለሁ” ወይም “እባርክሃለሁ”

እንድታፈሩና እንድትበዙ አደርጋለሁ

እነዚህ ሁለቱ ሀረጐች በትውልድ እንድበዙና ትልቅ ሕዝብ እንድሆኑ እግዚአብሔር እንደሚያደርጋቸው ያመለክታሉ (see doublet/ተመሣሣይ ትርጉም ያላቸውን ድርብ ቃላት ይመልከቱ)

ፍሬያማ አደርጋችኋለሁ

ዛፎች ብዙ ፍሬ እንደሚያፈሩ ብዙ ልጆች እንደሚኖራቸው እግዚአብሔር ይናገራል:: አት: ብዙ ልጆች እንድኖሩአችሁ አደርጋለሁ (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ለረጅም ጊዜ የተሰበሰበውን እህል ትበላላችሁ

“ለረጅም ጊዜ የምትመገቡት የተሰበሰበ ብዙ እህል ይኖራችኋል” ወይም “ለመሰብሰብና ለረጅም ጊዜ ለመብላት ብዙ እህል ይኖራችኋል”

Leviticus 26:11

ማደሪያዬን በመካከላችሁ አደርጋለሁ

መኖሪያዬን በአናንተ መካከል አደርጋለሁ

አልጸየፋችሁም

እቀበላችኋለሁ

በመካከላችሁ እመላለሳለሁ

በእነርሱ መካከል መመላለስ ከእነርሱ ጋር መኖርን ይወክላል አት ከእናንተ ጋር እኖራለሁ:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ቀንበራችሁን ሰብሬያለሁ

እግዚአብሔር ባርነታቸውን ከባድ ሥራን ለመሥራት በእንስሳት እንደሚደረግባቸው ቀንበር አድርጐ ይገልጻል:: ቀንበርን መስበር እነርሱን ነጻ ማውጣቱን ያመለክታል:: አት: ከባድ ሥራ እንድትሠሩ ከተደረጋችሁበት ምድር ነጻ አውጥቸአችኋለሁ:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 26:14

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ሕጉን ባይጠብቅ ምን እንደሚደርስበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

Leviticus 26:16

እነዚህን ነገሮች ቢያደርጉ

እነዚህ ነገሮች የሚለው ሀረግ በዘሌዋዊያን 26: 14-15 የተዘረዘሩ ነገሮችን ያመለክታል

የሚያስደነግጥ ትኩሳት አመጣባችኋለሁ

እዚህ ድንጋጤ እነርሱን ሊያስደነግጣቸው የሚችሉ ነገሮችን ያመለክታል:: አት: “የሚያስደነግጥ በሽታ አመጣባችኋለሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሕይወታችሁን እንዲቀስፍ አሠቃያለሁ

ቀስ በቀስ ሕይወታችሁን እወስዳለሁ ወይም ቀሰ በቀስ እንዲትሞቱ አደርጋለሁ:: ይህንን የሚያደርጉት ትኩሳትና በሽታዎች ናቸው፡፡

የሚትዘሩት በከንቱ ነው

በከንቱ ነው የሚለው ሀረግ ከሥራቸው ምንም አያገኙም ማለት ነው፡፡ አት፡ “ዘርን በከንቱ ትዘራላችሁ” ወይም “ዘርን ትዘራላችሁ ነገርግን ከዚያ ምንም አታገኙም” (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ፊቴን በእናንተ ላይ አከብድባችኋለሁ

ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር እግዚአብሔር ለመጨከን እንደወሰነ ይናገራል:: አት: እናንተን ለመጥላት በሀሳቤ ወስኛለሁ:: (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በጠላቶቻችሁ ድል እንዲትሁኑ አደርጋለሁ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ጠላቶቻችሁ ድል ያደርጓችኋል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 26:18

ሰባት እጥፍ

እዚህ ሰባት እጥፍ በእርግጥ በቁጥሩ ልክ ማለት አይደለም እግዚአብሔር የቅጣቱን መጠን በፍጹም እንደሚጨምር ያመለክታል (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ትዕቢታችሁን እሠብራለሁ

እንዳይታበዩ ኃይልን መጠቀም ትዕቢታቸውን እንደመሥበር ተደርጐ ተነግሮአል:: አት: “ባላችሁ ጉልበት የማሰማችሁን ትዕቢት ለማቆም እቀጣችኋለሁ” ወይም “በጉልበታችሁ እንዳትታበዩ እቀጣችኋለሁ”:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሰማያችሁን እንደብረት ምድራችሁንም አንደናስ አደርጋለሁ

ይህም እግዚአብሔር ዝናብ እንዳይዘንብ ያደርጋል ማለት ነው:: ይህም ሰዎች ዘርን እንዳይዘሩ ወይም እህልን እንዳያመርቱ ምድሪቱን ያደርቃል ማለት ነው:: (see Simile)

ኃይላችሁ በከንቱ ያልቃል

እጅግ ብዙ መሥራት ኃይል እስኪያልቅ ድረስ ሙሉ ጉልበትን ተጠቅሞ መሥራት ተደርጐ ተገልጾአል:: “በከንቱ ያልቃል” የሚለው ሀረግ እጅግ ብዙ ቢሠሩም ምንም አያገኙም ማለት ነው አት በከንቱ እጅግ ብዙ ትሠራላችሁ ወይም እጅግ ብዙ ትሠራላችሁ ነገርግን ብዙ በሠራችሁት ምንም አታገኙም ዘይቤያዊ አገላለጽ ወይም ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ

Leviticus 26:21

በእኔ ላይ ማመጽ ቢትቀጥሉ

“መቀጠል” ባሕሪይን ይገልጻል:: በእግዚአብሔር ላይ ማመጽ እግዚአብሔርን መቃወምን ወይም እርሱን አለመቀበልን ይወክላል አት: “በእኔ ላይ አታምጹ”

ሰባት እጥፍ መቅሠፍት እበትንባችኋለሁ

መበተን የሚለው ረቂቅ ስም መምታት በሚለው ግሥ ሊገለጽ ይችላል:: አት: ሳባት ጊዜ እመታችኋለሁ:: (ረቂቅ ስሞች ይመልከቱ)

ሰባት እጥፍ መቅሠፍት እበትንባችኋለሁ

እግዚአብሔር በእስራኤላዊያን ላይ መቅሰፍትን ማምጣቱ በመቅሠፍት እንደሚመታቸው ወይም እንደሚጐዳቸው ተደርጐ ተገልጾአል አት: “በእናንተ ላይ ሰባት እጥፍ በላይ መቅሠፍት አመጣለሁ” ወይም “ሰባት ጊዜ በላይ በአሠቃቂነት እቀጣችኋለሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሰባት እጥፍ

እዚህ ሰባት እጥፍ መደበኛ ሰባት ጊዜ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር የቅጣቱን አሠቃቂነት ይጨምራል ማለት ነው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እንደ ኃጢአታችሁ መጠን

“ኃጢአቶች” የሚለው ረቂቅ ስም “ኃጢአት” በሚለው ግሥ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “ምን ያህል ኃጢአት እንደሠራችሁ በዚያ መጠን” (ረቂቅ ስሞችን ይመልከቱ)

ልጆቻችሁን ይነጥቁአችኋል

“መንጠቅ” ማለት ማጥቃት ወይም አስገድዶ ማውጣት ነው ::አት: “ልጆቻችሁን የነጥቁአችኋል” ወይም “ልጆቻችሁን አስገድደው ይወስዱባችኋል” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

መንገዶቻችሁም ሰው አልባ ይሆናሉ

“ማንም በመንገዶቻችሁ ላይ አይራመድም” አልባ ይሆናሉ ማለት ማንም በዚያ አይኖርም ማለት ነው

Leviticus 26:23

በዚህ ሁሉ ግን

“እንደዚህ በሚቀጣበት ጊዜ” ወይም “እንደዚህ ቢቀጣችሁ”

ቅጣቴን ባትቀበሉ

ቅጣቱን መቀበል ለዚያ ተገቢ ምላሽ መስጠት ነው:: እዚህ ተገቢ ምላሽ እግዚአብሔርን መታዘዝ ነው:: አት: “አሁንም ቅጣቴን አልተቀበላችሁም” ወይም “አሁንም አልታዘዛችሁኝም” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

በማመጽም ቢትሄዱ

መሄድ ባሕሪይን ይወክላል:: እርሱን በማመጽ መሄድ ማለት እርሱን ማመጽ ወይም እርሱን መቃወም ማለት ነው አት፡ “አምጸውብኛል” ወይም “ተቃውመውኛል” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እኔም በማመጽ እሄዳለሁ

መሄድ ባሕሪይን ይወክላል:: እነርሱን በማመጽ መሄድ ማለት እነርሱን ማመጽ ወይም እርሱን መቃወም ማለት ነው አት፡ “ እኔም አምጽባችኋለሁ” ወይም “እቃወማቸዋለሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እኔ ራሴ ሰባት ጊዜ እቀጣችኋለሁ

ቁጥር 7 ፍጹምነትን ይወክላል:: አት: “እኔ ራሴ ብዙ ጊዜ እቀጣችኋለሁ” ወይም “እኔው ራሴ እጅግ አሠቃቂ በሆነ መንገድ እቀጣችኋለሁ”

ስለ ኃጢአታችሁ

“ኃጢአቶች” የሚለው ረቂቅ ስም “ኃጢአት” በሚለው ግሥ ሊገለጽ ይችላል:: አት: “በእኔ ላይ ኃጢአት መሥራታችሁን ስለቀጠላችሁ” (ረቂቅ ስሞችን ይመልከቱ)

Leviticus 26:25

በላያችሁ ሰይፍ አመጣባችኋለሁ

እዚህ “ሰይፍ” ሠራዊትን ወይም ከሠራዊት የሚደርስ ውጊያን ይወክላል:: አት: “የጠላት ሠራዊት አመጣበሃለሁ” ወይም “ጠላት እንዲዋጋህ አደርጋለሁ” ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

እበቀላችኋለሁ

እቀጣችኋለሁ

ቃል ኪዳኔን ስላፈረሳችሁ

“ቃልኪዳኔን ስላልታዘዛችሁ” ወይም “ቃል ኪዳኔን ስለማትታዘዙ”

በሚትሰበሰቡበት ጊዜ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ትሰበሰባላችሁ” ወይም “ትሸሻላችሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ለጠላትም እጅ አሳልፋችሁ ትሰጣላችሁ

እዚህ “እጅ” “ቁጥጥር ሥር” ማለት ሲሆን እናም በጠላት መሸነፍን ያመለክታል:: ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ለጠላቶቻችሁ እጅ አሳልፊ እሠጣችኋለሁ” ወይም “ጠላቶቻችሁ እንዲቆጣጠራችሁ አደርጋለሁ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የእንጀራችሁ እህል እንዲቋረጥ አደርጋለሁ

ሰዎች የሰበሰቡትን እህል ማጥፋት ወይም ሰዎች ይህን እንዳያገኙ ማድረግ የምግብ አቅርቦታቸውን ማቋረጥ ተደርጐ በተነግሮአል፡፡ አት፡ “የሰበሰባችሁትን እህል ባጠፋሁ ጊዜ” ወይም “ምግብን እንዳታገኙ ባደረግሁ ጊዜ” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ዐሥር ሴቶች በአንድ ምጣድ ላይ እንጀራ ይጋግራሉ

ይህም ጥቂት ዱቄት ከመኖር የተነሣ ብዙ ሴቶች የሚያመጡአቸው ለአንድ ምጣድ ብቻ እንደሚሆን ያመለክትል

Leviticus 26:27

ባትሰሙኝ

መስማት እርሱ ያለውን መታዘዝ ይወክላል አት ካለታዘዛችሁ ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

በአመጻችሁ ቢትሄዱ

መሄድ ባህሪይን ያመለክታል አንድን ሰው በማመጽ መሄድ እርሱን ማመጽ ወይም እርሱን መቃወም ነው፡፡ አት፡ ‘አመጻችሁብኝ” ወይም “ተቃወማችሁኝ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እኔ ደግም በቁጣ እሄድባችኋለሁ

መሄድ ባህሪይን ያመለክታል አንድን ሰው በማመጽ መሄድ እርሱን ማመጽ ወይም እርሱን መቃወም ነው፡፡ አት፡ “እኔ አምጽባችኋለሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ሰባት እጥፍ እቀጣችኋለሁ

እዚህ ሰባት እጥፍ መደበኛ ሰባት ጊዜን አያመለክትም እግዚአብሔር የቅጣቱን አሠቃነት መጠን ይጨምራል ማለት ነው (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 26:29

አፈርሳለሁ … እቆርጣለሁ… በድኖቻችሁን እጥላለሁ

እግዚአብሔር እነዚህን ለማድረግ ሠራዊትን ስለሚልክ ይህን ራሱ እንደሚያደርግ ተደርጐ ተናግሮአል አት “ለማፍረስ … ለመቁረጥ… በድኖቻችሁን ለመጣል ሠራዊትን እልካለሁ” ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

በድኖቻችሁ

ሙት አካሎቻችሁ

በድን በሆነው ጣዖቶቻችሁ

በሕይወት ኖረው እንደሞቱ አስመስሎ እግዚአብሔር ጣዖቶቻቸው በድን እንደሆኑ ይናገራል:: አት: “ሕይወት የሌላቸው ጣዖቶቻችሁ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

Leviticus 26:31

ከተሞቻችሁን አፈርሳለሁ መቅደሶቻችሁን ወና አደርጋለሁ

እነዚህ ሰዎች በእግዚአብሔር ፈንታ ጣዖቶቻቸውን ያመለኩባቸው ቦታዎች ናቸው

ጣፋጭ ሽታ ያለውን መሥዎዕቶቻችሁንም አልቀበልም

የእግዚአብሔር በመልካም መዓዛ ሽታ መደሰቱ መሥዋዕቱን በሚያቃጥሉ መደሰቱን ነው:: በዚህ ቦታ ግን ሰዎች መሥዋዕታቸውን ያቀጥላሉ ነገር ግን እግዚአብሔር በእነርሱ አልተደሰተም:: አት: “መሥዋዕቶችን ታቀርባላችሁ ወይም ታቃጥላላችሁ ነገር ግን እኔ አልደሰትባችሁም::” (ዘይቤያዊ አገላለጽ ይመልከቱ)

ሰይፈን መዝዤ አሳድዳችኋለሁ

ይህ ጠላቶችን ሊኮ እንደሚዋጋቸው ያመለክታል አት ሊዋጋችሁ የጠላት ሠራዊት እልክባችኋለሁ ወይም በሠይፎቻቸው ለመዋጋት የጠላት ሠራዊት እልክባችኋለሁ ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

ምድራችሁ ባድማ ከተሞቻችሁም ፍርስራሽ ይሆናሉ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ምድራችሁን ትተዋላችሁ እናም ጠላቶቻችሁ ከተሞቻችሁን ያፈርሳሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 26:34

ከዚያም ምድሪቱ በሰንበት ዓመትዋ ትደሰታለች

ሕዝቡ በየሰባት ዓመቱ ምድሪቱን ባለማረስ የሰንበትን ሕግ መታዘዝ አለባቸው:: እግዚአብሔር ምድሪቱን የሰንበትን ሕግና እረፍት እንደታዘዘ ሰው አድረጐ ይናገራል:: አት: “ከዚያም በሰንበት ሕግ መሠረት ምድሪቱ ታርፋለች” ወይም “ከዚያም የሰንበት ሕግ እንደሚያዝዘው ምድሪቱ አትታረስም” (ሰውኛ አገላለጽ ይመልከቱ)

ምድሪቱ ታርፋለች

ያልተታረሰውን መሬት እረፍት እንዳገኘ ሰው አድርጐ እግዚአብሔር ይናገራል:: ምድሪቱ መታረስ የለባትም::

ድንጋጤ እሰድባቸዋለሁ

በእነርሱ ልብ ድንጋጤን መስደድ እነርሱን ማሳፈርን ይወክላል:: አት: “እጅግ እንዲታፍሩ አደርጋችኋለሁ”:: (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ከሰይፍ እንደሚትሸሹ

ሰይፍ የሚወክለው ሰይፍን በመያዝ ሊገድል የተዘጋጀ ሰው ወይም ከጠላት ሠራዊት የሚሆን ውጊያን ነው:: አት: “በሰይፍ ከሚያሳድዳችሁ እንደሚትሸሹ” ወይም “ከጠላት ሠራዊት እንደሚትሸሹ” ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

Leviticus 26:37

አጠቃላይ መረጃ

እስራኤላዊያን በጉልበት ወደ ጠላቶቻቸው አገር በሚሄዱበት ጊዜ ምን እንደሚሆን እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ከሰይፍ እንደሚትሸሹ

ሰይፍ የሚወክለው ሰይፍን በመያዝ ሊገድል የተዘጋጀ ሰው ወይም ከጠላት ሠራዊት የሚሆን ውጊያን ነው:: አት: “በሰይፍ ከሚያሳድዳችሁ እንደሚትሸሹ” ወይም “ከጠላት ሠራዊት እንደሚትሸሹ” ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

በጠላቶቻቸው ፊት መቆም

በጠላቶች ፊት መቆምበጠላቶች ጥቃትና ውጊያ አለመውደቅን ያመለክታል:: አት: “በሚዋጉአችሁ ጊዜ ጠላቶቻችሁን ለመቋቋም” ወይም “ጠላቶቻችሁን መልሳችሁ ለመዋጋት” ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

የጠላቶቻችሁም ምድር ትቦጫጭቃችኋለች

እግዚአብሔር የጠላቶቻቸውን ምድር እስራኤላዊያንን እንደሚበላ እንደ አውሬ አድርጐ ይናገራል መቦጫጨቅ የሚለው ቃል አብዛኛዎቹ እስራኤላዊያን በዚያ እንደሚሞቱ ትኩረትን ይሰጣል አት በጠላቶቻችሁ ሀገር ትሞታላችሁ (See Personification/ አንድ ነገር አካል እንዳለው የመግለጽ ዘይቤ ይመልከቱ)

ከእናንተ የተረፉት

ሳይሞቱ የቀሩት

በኃጢአታቸው መንምነው ያልቃሉ

በኃጢአታቸው መንመነው ማለቅ በኃጢአታቸው ምክንያት መንምነው ማለቅን ያመለክታል

የአባቶቻቸው ኃጢአት

እዚህ አባቶች የቀደሙ አባቶቻቸውን ያመለክታል (See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

Leviticus 26:40

የአባቶቻቸው ኃጢአት

እዚህ አባቶች የቀደሙ አባቶቻቸውን ያመለክታል ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

ለእኔ ላይ ያልታመኑበትንና በእኔ ላይ ያመጹበትን

“ለእኔ ታማኝ ባልሆኑበት መንገድ እናም ለእነርሱ መልካም ሆኜ ሳለሁ በእኔ ላይ ያመጹበትን”

እኔን በማመጽ የሄዱበት

መሄድ ባህሪይን ያመለክታል አንድን ሰው በማመጽ መሄድ እርሱን ማመጽ ወይም እርሱን መቃወም ነው፡፡ አት፡ ‘አመጹብኝ” ወይም “ተቃወሙኝ” (ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

እኔ ጠላት እሆንባቸዋለሁ

ይህ እቃወማችኋለሁ የሚለውን ይወክላል አት እቃወማቸዋሁ(ዘይቤያዊ አነጋገር ይመልከቱ)

ያልተገረዘው ልባቸው ቢዋረድ

እዚህ “ያልተገረዘ ልብ” ሙሉውን ሰው ያመለክታል:: አት: “በልቤ ደንዳናነት ካለመዘዝ ፈንታ ራሳቸውን ቢያዋርዱ” (See Synecdoche)

በዚያን ጊዜ ከያዕቆብ ጋር የገባሁትን ኪዳኔን ከይስሐቅም ጋር የገባሁትን ኪዳኔን ደግሞም ከአብርሃም ጋር የገባሁትን ኪዳኔን አስባለሁ

እዚህ “አስባለሁ” ሆን ብሎ ማሰብን የሚገልጽ ፈሊጣዊ አባባል ነው:: እዚህ ቦታ ቃል ኪዳኑን እንደሚፈጽም ያመለክታል:: አት: በዚያን ጊዜ ከያዕቆብ ከይስሐቅና ከአብርሃም ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳኔን እፈጽማለሁ::

ምድሪቱን አስባታለሁ

እዚህ “አስባለሁ” ሆን ብሎ ማሰብን የሚገልጽ ፈሊጣዊ አባባል ነው:: እዚህ ስለምድሪቱ ያለውን ተስፋ ቃል እንደሚፈጽም ያመለክታል:: አት: “ስለምድሪቱ ያለውን ተስፋ ቃል እፈጽማለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገርና Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

Leviticus 26:43

ምድሪቱ ባዶ ተቀራለች

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “የእስራኤል ሕዝብ ምድራቸውን ይተዋሉ/ይለቅቃሉ ወይም ባዶ ያደርጋሉ” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በሰንበትዋ ትደሰታለች

እግዚአብሔር ስለምድሪቷ አንድ ሰው በእረፍቱ እንደሚደሰት አድረጐ ይናገራል ምክንያቱም በእርስዋ ላይ ዘርን የሚዘራ ወይም ሰብልን የሚያሳድግ አይኖርም ይህም ምድሪቱ ለም እንዲትሆን ያደርጋታል:: አት: “ምድሪቱ በሰንበታት ትጠቀማለች” (ሰውኛ አገላለጽ ይመልከቱ)

Leviticus 26:44

አጠቃላይ መረጃ

ይህ የመታዘዝ በረከቶችና ያለታዘዝ ቅጣቶችን እግዚአብሔር በሲና ተራራ ለሙሴ የተናገረውን መልእክት ያጠቃልላል

ከቀደሙ አባቶቻችሁ ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳን አስባለሁ

እዚህ “አስባለሁ” ሆን ብሎ ማሰብን የሚገልጽ ፈሊጣዊ አባባል ነው:: እዚህ ቦታ ቃል ኪዳኑን እንደሚፈጽም ያመለክታል:: አት: በዚያን ጊዜ ከአባቶቻችሁ ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳኔን እፈጽማለሁ:: (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

አሕዛብ እያዩ

ይህ የአሕዛብ ማወቅ ነው:: አት: “አሕዛብ እያወቁ” ወይም “አሕዛብ ይህን ያውቃሉ” ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)

አሕዛብ

የአዛብ ሕዝብን ይወክላል:: አት:” የአሕዛብ ሕዝብ” ( See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)


Chapter 27

1 ያህዌ ሙሴን ተናገረው እንዲህም አለ፣ 2 “ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ንገራቸው፣ ‹አንድ ሰው ለያህዌ ሰውን ለመስጠት የተለየ ስዕለት ቢሳል ተመጣጣን ዋጋ ለመክፈል ተከታዮን ዋጋዎች ተጠቀም፡፡ 3 ከዚያ እስከ ስልሳ አመት ዕድሜ ላለው ወንድ መደበኛው ዋጋ በቤ መቅደሱ ሰቅል መለኪያ ሃምሳ የብር ሰቅሎች ይሁን፡፡ 4 ለተመሳሳይ ዕድሜ ክልል ለሴቷ መደበኛው ዋጋ ሰላሳ ሰቅሎች ይሁን፡፡ 5 ከአምስት አመት እስከ ሀያ አመት ዕድሜ ለወንድ መደበኛው ዋጋ ሀያ ሰቅሎች ይሁን፣ ለሴቷ አስር ሰቅሎች ነው፡፡ 6 ከአንድ ወር ዕድሜ እስከ አምስት አመት ለወንድ መደበኛው ዋጋ አምስት የብር ሰቅሎች ይሁን፣ ለሴት ሶስት የብር ሰቅሎች ነው፡፡ 7 ከስልሳ አመት በላይ ለወንድ መደበኛው ዋጋ አስራ አምስት ሰቅሎች፣ ለሴት አስር ሰቅሎች ይሁን፡፡ 8 ነገር ግን ስዕለቱን የገባው ሰው መደበኛውን ዋጋ መክፈል ባይችል፣ በስለት የተሰጠው ሰው ወደ ካህኑ ይቅረብ፣ ካህኑም ያንን ሰው የተሳለው ሰው ሊከፍል በሚችል ዋጋ ይተምነዋል። 9 አንድ ሰው ለያህዌ እንስሳ መሰዋት ቢፈልግ፣ ያህዌ ያንን ቢቀበል፣ ከዚያ ያ እንስሳ ለእርሱ ይለያል፡፡ 10 ሰውዬው እንዲህ ያለውን እንስሳ መለወጥ ወይም መቀየር የለበትም፣ መልካሙን በመጥፎው ወይም መጥፎውን በመልካሙ አይቀይርም፡፡ አንዱን እንስሳ በሌላው ቢለውጥ፣ ያ እንስሳና የተለወጠው ሁለቱም ንጹህ ይሆናሉ፡፡ 11 ሆኖም፣ ሰውዬው ለያህዌ ሊሰጥ የተሳለው ንጹህ ካልሆነ ስለዚህ ምክንያት ያህዌ ያንን አይቀበልም፣ ከዚያ ሰውዬው እንስሳውን ወደ ካህኑ ማምጣት አለበት፡፡ 12 ካህኑ በገበያው የእንስሳ ዋጋ ይተምነዋል፡፡ ማናቸውም ካህኑ ለእንስሳው የሰጠው ዋጋ፣ ያ የእንስሳው ዋጋ ይሆናል፡፡ 13 እናም ባለቤቱ እንስሳውን ሊዋጅ ቢፈልግ፣ በሚዋጅበት ዋጋ ላይ አንድ አምስተኛውን ጨምሮ ይዋጀው፡፡ 14 አንድ ሰው ቤቱን ለያህዌ መቀደስ ሲፈልግ፣ ካህኑ የቤቱን ዋጋ ይተምናል፡፡ ማናቸውም ካህኑ የተመነው ዋጋ ያ የዚያ ቤት ዋጋ ነው፡፡ 15 ነገር ግን ባለቤቱ ቤቱን ቢለይና በኋላ ሊዋጀው ቢፈልግግ በሚዋጅበት ዋጋ ላይ አንድ አመስተና ይጨመር፣ እናም ከዚያ እንደገና የእርሱ ይሆናል፡፡ 16 አንድ ሰው ከመሬቱ ለያህዌ ለመለየት ቢፈልግ፣ የመሬቱ ዋጋ ግምት ለመዝራት በሚያስፈልገው ፍሬ መጠን ይተመናል፡፡ አንድ ሆሜር መስፈሪያ ገብስ ሃምሳ የብር ሰቅሎች ያወጣል፡፡ 17 እርሻውን በኢዮቤልዩ አመት ቢለይ፣ የተገመተው ዋጋ ይፀናል፡፡ 18 እርሻውን ከኢዮቤልዩ በኋላ ቢለይ ግን፣ ካህኑ የእርሻ መሬቱን ዋጋ እስከ ቀጣዩ የኢዮቤልዩ አመት ድረስ ባሉ አመታት ቁጥር ያሰላና የተገመተው ዋጋ ይቀነሳል፡፡ 19 እርሻውን የለየው ሰው ሊዋጀው ቢፈልግ፣ በተገመተው ዋጋ ላይ አንድ አምስተኛ ይጨምራ፣ እናም መሬቱ ተመልሶ የእርሱ ይሆናል፡፡ 20 እርሻውን ካልዋጀ ወይም ለሌላ ሰው ሸጦት ከሆነ፣ ከዚያ በኋላ ተመልሶ ሊዋጅ አይችልም፡፡ 21 ይልቁንም፣ እርሾው፣ በኢዮቤልዩ ተመልሶ ሲለቀቅ ሙሉ ለሙሉ ለያህዌ እንደተሰተ እርሻ ሁሉ ለያህዌ ቅዱስ ስጦታ ይሆናል፡፡ የካህናቱ ንብረት ይሆናል፡፡ 22 አንድ ሰው የገዛውን መሬት ለያዌ ቢለይ፣ ነገር ግን መሬቱ ከሰውዬው ቤተሰቦች መሬት ውስጥ ባይሆን፣ 23 ካህኑ የእርሻውን ዋጋ እስ ኢዮቤልዩ አመት ድረስ ባለው ጊዜ መተን ይተምናል፣ ሰውዬውም ዋጋውን በዚያ ቀን ለያህዌ ቅዱስ ስጦታ አድርጎ ይከፍላል፡፡ 24 በኢዮቤልዮ አመት፣ እርሻው ከገዛው ሰው ተወስዶ ወደ መሬቱ የቀድሞ ባለቤት ይመለሳል፡፡ 25 የሚተመኑ ዋጋዎች ሁሉ በመቅደሱ ሰቅል ዋጋ ሊተመኑ ይገባል፡፤ ሃያ ጌራ ከአንድ ሰቅል ጋር እኩል ነው፡፡ 26 ከእንስሳት በመጀመሪያ የሚወለደው ግን አስቀድሞም ቢሆነ የያህዌ ነው፣ ማንም ሰው ሊቀድሰው አይችልም በሬም ይሁን በግ የያህዌ ነው፣ ማንም ሰው ሊቀድሰው አይችልም በሬም ይሁን በግ የያህዌ ነው 27 ንጹህ ያልሆነ እንስሳ ከሆነ፣ ባለቤቱ በተመገተው ዋጋ መልሶ ይግዛውው ደግሞም ከዋጋው በላይ አንድ አምስተኛ ይጨምርበት፡፡ እንስሳው ካልተዋጀ፣ በተተመነው ዋጋ ይሸጥ፡፡ 28 ሆኖም፣ አንድ ሰው ለያህዌ ከለየው ሰውም ሆነ ወይም እንስሳ፣ ወይም የቤተሰቡ ርዕስት ምንም ነገር አይሽጥ ወይም አይዋጅ ማናቸውም የተለየ ነገር ለያህዌ ቅዱስ ነው፡፡ 29 እንዲጠፋ ለተለየ ሰው ምንም መዋጃ አይከፈልለትም፡፡ ያ ሰው መገደል አለበት፡፡ 30 አስራት ሁሉ፣ በምድሪቱ ላይ የበቀለ ሰብልም ሆነ ወይም የዛፍ ፍሬ የያህዌ ነው፡፡ ለያህዌ የተቀደሰ ነው፡፡ 31 አንድ ሰው ከአስራቱ አንዳች ቢዋጅ፣ በዋጋው ላይ አንድ አምስተኛ ይቸምር፡፡ 32 ከመንጋ ወይም ከከብት አስራት ሁሉ፣ ከእረኛው በትር ስር የሚያልፍ ሁሉ፣ ከአስር አንዱ ለያህዌ ይለይ፡፡ 33 እረኛው የተሸለውን ወይም የከፋውን እንስሳ አይፈልግም፣ ደግሞም አንዱን በሌላው አይተካ፡፡ ቢለውጠው እኗን፣ የተለወጠውና የሚለወጠው ሁለቱም የተቀደሱ ይሆናሉ፡፡ ሊዋጅ አይችልም፡፡” 34 ያህዌ በሲና ተራራ ለሙሴ የሰጣቸው ለእስራኤላውያን የተሰጡ ትእዛዛት እነዚህ ናቸው፡፡



Leviticus 27:1

ማንኛውም ሰው ለእግዚአብሔር ልይ ስእለት ቢሳል

በዚህ ዐውድ ስእለቱ ራሱን ወይም ሌላን ሰው ለእግዚአብሔር ለማቅረብ ይሆናል፡፡ ይህ ግልጽ ተደርጐ ሊነገር ይችላል፡፡ አት: “ማንም አንድን ሰው ለእግዚአብሔር ለማቅረብ ቢሳል” (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

የሚከተሉትን ተመጣጣኝ ዋጋ መክፈል

ለእግዚአብሔር ሰውን በመስጠት ፈንታ የተወሰነ ብር ይክፈል አት በሰው ፈንታ እንደሚከተሉት ተመጣጣኝ ዋጋ መሠረት ለእግዚአብሔር ስጦታ ያቅርብ ወይም በሰው ፈንታ እንደሚከተሉት የነሐስ መጠን ይክፈል (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

Leviticus 27:3

መደበኛ ዋጋ

“የሚከፈል የዋጋ መጠን” ወይም “መከፈል ያለበት”

ሃያ ስድሳ ሃምሳ ሠላሣ

2ዐ 6ዐ 5ዐ 3ዐ ቁጥሮችን ይመልከቱ

ሃምሳ ሰቅል ብር

የዘመናዊ ሚዛኖች መለኪያ መጠቀም ካስፈለገ ሁለቱ መንገዶች እነሆ:: አት: “ሃምሳ ሰቅል ብር እያንዳንዳቸው አሥር ግራም የመዘናሉ” ወይም “5ዐዐ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ ሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያየ ሚዛን ያላቸው ሰቅሎች አሉ:: በተቀደሰው የመገናኛው ድንኳን ውስጥ ሰዎች በመጠቀም ያለባቸው ይህን ሚዛን ነው:: ይህም 11 ግራም ይመዝናል:: አት: “በመቅደሱ የሚጠቀሙበትን ዓይነት ሰቅል ይጠቀሙ” ወይም “ብርን ሲመዝኑ በመቅደሱ የሚጠቀሙበትን ሚዛን ይጠቀሙ” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

ሠላሣ ሰቅል

የዘመናዊ ሚዛኖች መለኪያ መጠቀም ካስፈለገ ሁለቱ መንገዶች እነሆ:: አት: “ሠላሣ ሰቅል ብር እያንዳንዳቸው አሥር ግራም የመዘናሉ” ወይም “3ዐዐ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

Leviticus 27:5

አምስት ሃያ አሥር ሶስት

5 20 10 3 ቁጥሮችን ይመልከቱ

መደበኛ ዋጋ

“የሚከፈል የዋጋ መጠን” ወይም “መከፈል ያለበት”

ሃያ ሰቅል

የዘመናዊ ሚዛኖች መለኪያ መጠቀም ካስፈለገ ሁለቱ መንገዶች እነሆ:: አት: “ሃያ ሰቅል ብር እያንዳንዳቸው አሥር ግራም የመዘናሉ” ወይም “ሁለት መቶ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

ለሴት ከሆነ አሥር ሰቅል

እድሜ እና ግምቱ የሚሉ አዚህ ተዘለዋል:: ነገርግን ታሳቢ እንደሆኑ መረዳት ተገቢ ነው:: አት “ይህን እድሜ ለሆነ ሴት ግምቱ አሥር ሰቅል ነው”(መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል

የዘመናዊ ሚዛኖች መለኪያ መጠቀም ካስፈለገ ሁለቱ መንገዶች እነሆ:: አት: “አሥር ሰቅል ብር እያንዳንዳቸው አሥር ግራም የመዘናሉ” ወይም “አንድ መቶ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

አምስት ሰቅል

የዘመናዊ ሚዛኖች መለኪያ መጠቀም ካስፈለገ ሁለቱ መንገዶች እነሆ:: አት: “አምስት ሰቅል ብር እያንዳንዳቸው አሥር ግራም የመዘናሉ” ወይም “ሃምሳ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

ሶስት ሰቅል

የዘመናዊ ሚዛኖች መለኪያ መጠቀም ካስፈለገ ሁለቱ መንገዶች እነሆ:: አት: “ሶስት ሰቅል ብር እያንዳንዳቸው አሥር ግራም የመዘናሉ” ወይም “ሠላሣ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

Leviticus 27:7

ስድሳ አመት ዕድሜና ከዚያ በላይ

ስድሳ ዓመትና ከዚያ በላይ ዕድሜ

ስድሳ አሥራ አምስት አሥር

6ዐ 15 1ዐ ቁጥሮችን ይመልከቱ

አሥራ አምስት ሰቅል

የዘመናዊ ሚዛኖች መለኪያ መጠቀም ካስፈለገ ሁለቱ መንገዶች እነሆ:: አት: “አሥራ አምስት ሰቅል ብር እያንዳንዳቸው አሥር ግራም የመዘናሉ” ወይም “ አንድ መቶ ሃምሳ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

ለሴት ከሆነ አሥር ሰቅል

እድሜ እና ግምቱ የሚሉ አዚህ ተዘለዋል:: ነገርግን ታሳቢ እንደሆኑ መረዳት ተገቢ ነው:: አት “ይህን እድሜ ለሆነ ሴት ግምቱ አሥር ሰቅል ነው”(መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ): Ellipsis/ ዐውዱ ሊገልጽ የሚችሉ ቃላትን ወይም አባባሎችን የመደበቅ ወይም የመዝለል ዘይቤ ይመልከቱ)

የተሰጠው ሰው ለካህኑ መቅረብ አለበት

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “የሚሰጠውን ሰው ለካህኑ ማቅረብ አለበት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 27:9

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ለሙሴ ይናገራል

ለእርሱ ለያቸው

ለያህዌ ለያቸው

እርሱንና እርሱን የሚተካውን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “እርሱንና በእርሱ ምትክ የሚቀርበውን” ወይም “ሁለቱ እንስሶች” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 27:11

የረከሰ ከሆነ እግዚአብሔር አይቀበለውም

እግዚአብሔር እንስሳውን መሥዋዕት አድርጐ ካልተቀበለ ያ እንስሳ በአካል የረከሰ ወይም የቆሸሸ ተብሎ ተገልጾአል :: የተለየ ዓይነት ወይም እንከን ያለበት እንስሳ ስለሆነ ርኩሰ ተብሎአል አት በእርግጥ እግዚአብሔር የማይቀበለው ነው

የገበያ ዋጋ

ይህ አንድ ሰው ሲሸጥ ወይም ሲገዛ እንስሳው የሚያወጣው መደበኛ ዋጋ ነው

ሊዋጀው ቢፈልግ

እንደገና ሊገዛው ቢፈልግ

Leviticus 27:14

የዋጋውን አንድ አምስተኛ በዋጋው ላይ ይጨምር

አምስተኛ ከአምስት እኩል ክፍሎች አንዱን ነው አት የቤቱን ዋጋ በአምስት ይክፈለው ከእነዚህ እኩል ክፍሎች የአንዱን ክፍል በላዩ ላይ ይጨምር እናም ሁሉን ይክፈል፡፡ (ክፍልፋዮችን ይመልከቱ)

Leviticus 27:16

በሚያስፈልገው ዘር መጠን

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ሰውየው ሊዘራ የሚያስፈልገው ዘር መሠን” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

የአንድ ሆሜር ገብስ ዘር ዋጋ

እዚህ አንድ ሆሜር ገብስ ዘር የሚወክለው አንድ ሆሜር ገብስ ሊዘራበት የሚችልበትን መሬት ነው:: አት: “አንድ ሆሜር ገብስ ዘር በሙሉ ሊዘራበት የሚጠይቅ መሬት ዋጋ” ወይም “አንድ ሆሜር የገብስ ዘር የሚወስድ መሬት” ዋጋ (See Metonymy/ ተዛማጅ ባህሪይ የሚገልጹ ምትክ ቃላትና አባባሎች ይመልከቱ)See Metonmy)

ሆሜር

አንድ ሆሜር 22 ሊትር ነው (መጽሐፍ ቅዱሳዊ መለኪያዎችን ይመልከቱ)

ሃምሳ ሰቅል ብር

ዘመናዊ የክብደት መለኪያዎችን መጠቀም ካስፈለገ ሁለት መንገዶች አሉ:: አት: “የሃምሳ ሰቅል ብር የእያንዳንዱ ሰቅል ዋጋ አሥር ግራም ነው” ወይም “አምስት መቶ ግራም ብር” (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችንና ቁጥሮችን ይመልከቱ)

Leviticus 27:17

የኢዩቤልዩ ዓመት

ይህ በየ5ዐ ዓመት ይደረጋል:: በዘሌዋዊያን 25: 1ዐ “ኢዩቤልዩ” እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ

የተተመነው ዋጋ ልክ ነው

“የተተመነው ዋጋ ይጸናል” ወይም “የተተመነው ዋጋ ተመሣሣይ ሆኖ ይጸናል” አት: “ዋጋው ተመሣሣይ ይሆናል” ወይም “የዋጋው መጠን ሙሉ ይሆናል” (ዘይቤይዊ አነጋገር ይመልከቱ)

የተተመነው ዋጋ ይቀነሳል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ከተተመነው ዋጋ ይቀንሳል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 27:19

ሊዋጅ አይቻልም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ሊዋጀው አይችልም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እርሻውን ባይዋጅ

እርሻውን የሚዋጅበት ጊዜ ግልጽ ሊደረግ ይችላል አት ከኢዩቤልዩ ዓመት በፊት እርሻውን ባይዋጅ (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

በኢዩቤልዩ ዓመት

“በመመለስ ዓመት” ወይም “መሬት የሚመለስበትና ባሪያዎች ነጻ የሚወጡበት ዓመት” ይህ አይሁዳዊያን መሬትን ለባለመሬቱ የሚመልቱበትና ለባሪያዎች ነጻነትን የሚያውጁበት ዓመት ነው:: በዘሌዋዊያን 25:13 ይህን እንዴት እንደተረጐሙ ይመልከቱ::

ለእግዚአብሔር እንደተሰጠ ይቆጠር

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “አንድ ሰው ሙሉ በሙሉ ለእግዚአብሔር ይሰጠዋል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 27:24

ለሸጠው ሰው …. ቀድሞ በለርስት ለነበረው

እነዚህ ሁለቱ ሀረጐች ተመሣሣይ ሰው ያመለክታሉ:: የታወቀው መንገድ መሬቱ የተገዛው ከባለርስቱ ነው

ከተገዛው ሰው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “የሸጠው ሰው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ዋጋው ይተመናል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ካህኑ ዋጋውን ይተምናል” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ ሰቅል ልክ

የተለያዩ የሰቀል ዓይነቶች አሉ ይህ በቅዱስ ድንኳን መቅደስ ሰዎች ከሚጠቀሙት አንዱ ነው መጽሐፍ ቀዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ

አንዱ ሰቅል ሃያ ጌራ ነው

የዚህ ዐረፍተ ነገር ዋና ዓላማ የመቅደሱ ሰቅል ምን ያህል እንደሚመዝን ለመናገር ነው፡፡ ጌራ እስራኤላዊያን ከሚጠቀሙት ሚዛኖች ወይም መለኪያዎች አነስተኛው ነው አት አንድ ሰቅል ሃያ ጌራ ነው፡፡ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማዛኖችን ይመልከቱ)

ሃያ ጌራ አንድ ሰቅል ነው

ዘመናዊ ሚዛኖችን መጠቀም ካስፈለገ ሁለት መንገዶች አሉ፡፡ አንድ ሰቅል አሥር ግራም ይመዝናል፡፡ (ቁጥሮችንና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሚዛኖችን ይመልከቱ)

Leviticus 27:26

ማንም… መቀደስ አይችልም

“ማንም ለእግዚአብሔር መቀደስ አይችልም”

በተተመነው ዋጋ ላይ አንድ አምስተኛ ጨመሮ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “በዋጋው ላይ አንድ አምሰተኛ ይጨምር” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እንስሳው ካለተዋጀ

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ሰውየው እንስሳውን ካልዋጀው” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 27:28

ለእግዚአብሔር የተሰጠ ማንኛውም ነገር ሰውም ሆነ እንስሳ ወይም በውርሰ የተገኘ መሬት አይሸጥም አይዋጅምም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ካለው ለእግዚአብሔር የሰጠውን ማንኛውም ነገር ሰውም ሆነ እንስሳ ወይም በውርስ የተገኘ መሬት አይሸጥም አየዋጅምም” ወይም “አንድ ሰው ካለው ለእግዚአብሔር የሰጠውን ማንኛውም ነገር ሰውም ሆነ እንስሳ ወይም በውርስ የተገኘ መሬት አይሸጥም አይዋጅምም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር የተሰጠ ማንኛውም ነገር እጅግ የተቀደሰ ነው

“ማንኛውም ሰው ለእግዚአብሔር የሰጠው ማንኛውም ነገር ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ነው”

የመዋጀት ካሣ አይከፈልም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ማንም የመዋጀት ካሣ አይከፍልም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

እንዲጠፋ የተወሰነ ማንም ሰው

ለምን ሰውየው እንዲጠፋ እንደተወሰነ ግልጽ መደረግ አለበት፡፡ አት ከኃጢአቱ የተነሣ እንዲጠፋ እግዚአብሔር የወሰነው ማንኛውም ሰው (ግምታዊ እውቀት ወይም ጥልቅ መረጃ ይመልከቱ)

ያ ሰው ይገደል

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ያን ሰው እንዲገደል አድርጉ” ወይም “ያን ሰው ግደሉት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 27:30

አንድ ሰው ከአሥራቱ ማንኛውንም ቢዋጅ

“አንድ ሰው ከአሥራቱማንኛውንም መዋጀት ቢፈልግ”

Leviticus 27:32

ማንኛውም ከእረኛ በትር በታች የሚያልፍ

ይህ እንስሳትን የማቆጥሩበትም መንገድ ያመለክታል:: አት: “የእረኛን በትር ከፍ በማድረግ በሥሩ ወደ ሌላኛው ጐን እንስሳት እንዲያልፉ በማድረግ በምትቆጥሩበት ጊዜ” ወይም “እንስሳትን በምትቆጥሩበት ጊዜ” (See Metonymy)

አንድ አሥረኛው ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ነው

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “አንድ አሥረኛውን ለእግዚአብሔር ቀድሱት” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

አንድ አሥረኛ

አያንዳንዱ አሥረኛው

ይህና ሌላው የተተካው

ሁለቱም እንስሳት

አይዋጅም

ይህ ተሻጋሪ ግሥ በያዘ መንገድ ሊተረጐም ይችላል:: “ሊዋጀው አይችልም” ወይም “መልሶ ሊገዛው አይችልም” (ተሻጋሪ ግሥ ወይም የማይሻገር ግሥ የያዘ ዐረፍተ ነገር ይመልከቱ)

Leviticus 27:34

ትእዛዛት እነዚህ ናቸው

ይህ ማጠቃለያ ዐረፍተ ነገር ነው:: በቀደሙት ምዕራፎች የተሰጡ ወይም የተነገሩ ትእዛዛትን ያመለክታል::


Book: Numbers


Numbers

Chapter 1

1 ያህዌ በሲና ምድረ በዳ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ሙሴን ተናገረው፡፡ ይህ የሆነው የእስራኤል ህዝብ ከግብጽ ምድር በወጣበት በሁለተኛው አመት በሁለኛው ወር በመጀመሪያው ቀን ነበር፡፡ ያህዌ እንዲህ አለ፣ 2 “በየነገዱ፣ በየአባቶቻቸው ቤተሰቦች የእስራኤል ወንዶች ቆጠራ ይደረግ፡፡ በስም ቁጠራቸው፡ እያንዳንዱ ወንድ፣ በሰው ቁጠር፣ 3 ሀያ አመት የሞላው ወይም ከዚያ በላይ የሆነ ወንድ ሁሉ ይቆጠር፡፡ ለእስራኤል ወታደር ሆኖ ሊዋጋ የሚችለውን ሁሉ ቁጠር፡፡ አንተና አሮን በታጣቂ ቡድኖቻቸው የወንዶችን ቁጥር መዝግቡ፡፡ 4 ከእያንዳንዱ ጎሳ አንድ ሰው፣ የነገድ አለቃ ከአንተ ጋር የጎሳው መሪ ሆኖ ያገልግል፡፡ እያንዳንዱ መሪ ለጎሳው የሚዋጉትን ወንዶች ይምራ፡፡ 5 ከአንተ ጋር ሆነው መዋጋት ያለባቸው መሪዎች ስሞቻቸው እነዚህ ናቸው፡ ከሮቤል ጎሳ፣ የሰዲዮር ልጅ ኤሊሱር፣ 6 ከስምዖን ጎሳ የሱሪሰዳይ ልጅ ሰለሚኤል፤ 7 ከይሁዳ ጎሳ፣ የአሚናዳብ ልጅ ነአሶን፤ 8 ከይሳኮር ጎሳ የሶገር ልጅ ናትናኤል፤ 9 ከዛብን ጎሳ፣ የኬሎን ልጅ ኤልያብ፤ 10 ከኤፍሬም ጎሳ፣ የዮሴፍ ልጅ፣ የዓሚሁድ ልጅ ኤሊሳማ፤ ከምናሴ ጎሳ፣ የፍዳሱር ልጅ ገማልኤል፤ 11 ከብንያም ጎሳ የዮሴፍ ልጅ፣ የጌዲዮን ልጅ አቢዳን፤ 12 ከዳን ጎሳ የአሚሳዳይ ልጅ አኪዔዘር፣ 13 ከአሴር ጎሳ፣ የኤክራን ልጅ ፉግኤል፣ 14 ከጋድ ጎሳ የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ፤ 15 እና ከንፍታሌም ጎሳ፣ የዔናን ልጅ አኪሬ” ናቸው፡፡ 16 ከሕዝቡ የተመረጡት ወንዶች እነዚህ ነበሩ እነርሱ የአባቶቻቸውን ጎሳዎች ይመራሉ፡፡ በእስራኤል የነገዶች መሪዎች ነበሩ፡፡ 17 ሙሴና አሮን በስም የተመዘገቡትን እነዚህን ወንዶች ወሰዱ፣ 18 ከእዚህ ወንዶች ጋር በሁለተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን የእስራኤል ወንዱን ሁሉ ሰበሰቡ፡፡ ከዚያም ሃያ አመት የሞላውና ከዚያ በላይ የሆነ እያንዳንዱ ወንድ የትውልድ ሐረጉን ተናገረ፡፡ እያንዳንዱ የነገዱን ስም እና የትውልድ ሐረጉን መጥራት ነበረበት፡፡ 19 ከዚያም ሙሴ በሲና ምድረ በዳ ያህዌ እንዲያደርገው ባዘዘው መሠረት ቁጥራቸውን መዘገበ፡፡ 20 የእስራኤል በኩር ከሆነው ከሮቤል ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉት ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 21 ከሮቤል ጎሳ 46500 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 22 ከስምኦን ትውልዶች ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉት ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 23 ከስምዖን ጎሳ 59300 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 24 ከጋድ ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 25 ከጋድ ጎሳ 45650 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 26 ከይሁዳ ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስም ተቆጠሩ፡፡ 27 ከይሁዳ ጎሳ 7460 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 28 ከይሳኮር ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 29 ከይሳኮር ጎሳ 54400 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 30 ከዛብሎን ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 31 ከዛብን ጎሳ 57400 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 32 ከዮሴፍ ልጅ ከኤፍሬም ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 33 ከኤፍሬም ጎሳ 40500 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 34 ከዮሴፍ ልጅ ከምናሴ ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፤ 35 ከምናሴ ጎሳ 32200 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 36 ከብንያም ትውልዶች ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፤ 37 ከብንያም ጎሳ 35400 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 38 ከዳን ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 39 ከዳን ጎሳ 62700 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 40 ከአሴር ትውልዶች፣ ወደ ጦርት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 41 ከአሴር ጎሳ 41500 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 42 ከንፍታሌም ትውልዶች፣ ወደ ጦርነት መሄድ የሚችሉ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ የሆኑ ወንዶች ሁሉ ከየጎሳቸውና፣ ከየቤተሰባቸው መዛግብት እያንዳንዳቸው በስማቸው ተቆጠሩ፡፡ 43 ከንፍታሌም ጎሳ 53400 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 44 ሙሴና አሮን እነዚህን ወንዶች ሁሉ አስራ ሁለቱን የእስራኤል ጎሳዎች ከሚመሩ አስራ ሁለት ሰዎች ጋር ሆነው ቆጠሩ፡፡ 45 ስለዚህም ሃያ አመትና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላቸው ለጦርነት መውጣት የሚችሉ የእስራኤል ወንዶች ሁሉ በየቤተሰባቸው ተቆጠሩ፡፡ 46 የቆጠሯቸው ወንዶች 603550 ናቸው፡፡ 47 ከሌዊ ትውልድ የሆኑት ግን አልተቆጠሩም፣ 48 ምክንያቱም ያህዌ ሙሴን እንዲህ ብሎት ነበር፣ 49 “የሌዊን ጎሳ አትቆጥርም ወይም እነርሱን በእስራኤል ህዝብ ቆጠራ ውስጥ አታስገባቸው፡፡ 50 ይልቁንም፣ ሌዋውያንን የቃልኪዳኑን ስርዓቶች በቤተመቅደስ እንዲፈጽሙ መድባቸው፣ እንደዚሁም በቤተመቅደስ ውስጥ የሚገኙ መገልገያዎችንና ማናቸውንም ነገሮች እንዲንከባከቡ ሹማቸው፡፡ ሌዋውያን ጽላቱን ይሸከሙ፣ እንዲሁም የቤተመቅደሱን ዕቃዎች ይሸከሙ፡፡ 51 ቤተመቅደሱ ወደ ሌላ ስፍራ በሚንቀሳቀስበት ጊዜ፣ ሌዋውያኑ ይንቀሉት፡፡ ቤተመቅደሱ ሲተከል፣ ሌዋውያን ይትከሉት፡፡ ወደ ቤተ መቅደሱ የሚጠጋ ማናቸውም እንግዳ ይገደል፡፡ 52 እስራኤላውያን ድንኳኖቸውን ሲተክሉ፣ እያንዳንዱ ሰው ወደ ራሱ የጦር ቡድን ዐርማ አጅግ ቀርቦ ይስራ፡፡ 53 ሆኖም፣ ሌዋውያኑ ቁጣዬ በእስራኤላውያን ላይ እንዳይሆን ድንኳናቸውን በቃል ኪዳኑ ማደሪያ ዙሪያ ይትከሉ፡፡ ሌዋውያኑ የቃልኪዳኑን ማደሪያ ሀላፊዎች ናቸው፡፡” 54 እስራኤላውያን እነዚህን ሁሉ ነገሮች አደረጉ፡፡ ያህዌ በሙሴ በኩል ያዘዛቸውን ነገሮች ሁሉ አደረጉ፡፡



Numbers 1:1

እግዚአብሔር

ይህ ስም በብሉይ ኪዳን ዘመን ለሕዝቡ የገለጠው የራሱ ሥም ነው፡፡እግዚአብሔር የሚለውን ቃል በሚመለከት ትርጉሙን ለማወቅ የትርጉም ቃላቱን ገፅ ይመልከቱ፡፡

በሁለተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን

በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት ይሄ ሁለተኛ ወር ነው፡፡በምዕራባውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት የመጀመሪያው ቀን የካቲት አጋማሽ አካባቢ ላይ የሚውል ነው፡፡(የዕብራውያን የቀን ወራትንና ተከታታይ ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሁለተኛው ዓመት

“ሁለተኛው ዓመት” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

በየስማቸው ቁጠሩ

ይሄ ማለት የወንዶቹን ስም በመመዝገብ ቁጥራቸውን ማወቅ ማለት ነው፡፡“የእያንዳንዱን ሰው ሥም በመፃፍ ቁጠሯቸው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ሃያ ዓመት ዕድሜ ያላቸው

“የሃያ ዓመት ዕድሜ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ከሠራዊታቸው አንፃር የወንዶችን ቁጥር ቁጠር

ይሄ ወንዶች በየጦር ክፍሉ መመደባቸውን ያመለክታል፡፡

Numbers 1:4

የአባቶች ቤት አለቃ

“ የአንድ ነገድ መሪ”

ከእናንተ ጋር ይሁን

“ይርዳችሁ” ኤሊሱር፤ሰለሚኤል፤ነአሶን፤ናትናኤል እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ) ፡

Numbers 1:7

እግዚአብሔር የነገድ መሪዎችን ስም መዘርዘር ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር የነገድ መሪዎችን ስም መዘርዘር ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:10

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር የነገድ መሪዎችን ስም መዘርዘር ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:12

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር የነገድ መሪዎችን ስም መዘርዘር ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ) ፡

Numbers 1:16

የተመረጡት ሰዎች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር የመረጣቸው ሰዎች” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:17

እነዚህን ሰዎች ውሰዷቸው

“እነዚህ ሰዎች አንድ ላይ እንዲሳበሰቡ አድርጓቸው”

በየስማቸው የተጠሩትን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”ስማቸውን የመዘገቧቸው ሰዎች” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በሁለተኛው ወር የመጀመሪያ ቀን

ይሄ በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት ሁለተኛው ወር ነው፡፡በምዕራባውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት የመጀመሪያው ቀን የሚውለው መጋቢት ወር መካከል አካባቢ ይሆናል፡፡ይህንን በዘኁልቁ 1፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(የዕብራውያን ወርንና የቅደም ተከተል ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ከዚያም እያንዳንዱ ሰው ትውልዱን አወቀ…የወገኑንና የአባቶቹን ቤት በየስማቸው ትውልዱን መናገር ነበረበት፡፡

በመሠረቱ ሁለተኛው ዓረፍተ ነገር ከመጀመሪያው ዓረፍተ ነገር ጋር ተመሣሣይነት ያለው ሲሆን እንዲጨመር የተደረገውም ጉዳዩን የበለጠ ግልፅ ለማድረግ ተበሎ ነው፡፡ (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

በየስማቸው መጥራት ነበረበት

“በየስማቸው መጥራት” የሚለው የሚያመለክተው “መናገርን.” ነው፡፡ ”እያንዳንዱ ሰው መናገር ነበረበት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:20

እንደየስማቸው ተቆጥረው ነበር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”ስሞቹን ሁሉ ቆጠሩ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ ጦርነት ለመሄድ የሚችሉ

“ወደ ጦርነት ለመሄድ አቅም ያለው”

46,500 ሰዎች

“አርባ ስድስት ሺህ አምስት መቶ ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:22

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ) 59,300

Numbers 1:24

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡ 20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

46,650

“አርባ ስድስት ሺህ ስድስት መቶ ሃምሳ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:26

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡ 20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

74,600

“ሰባ አራት ሺህ ስድስት መቶ ወንዶች” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:28

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡ 20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

54,400

“ሃምሳ አራት ሺህ አራት መቶ ወንዶች” (ኦሪት ዘኁልቁን ይመልከቱ)

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

57,400 ወንዶች

“ሃምሳ ሰባት ሺህ አራት መቶ ወንዶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:30

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

40,500

“አርባ ሺህ አምስት መቶ ወንዶች” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:32

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

40,500

“አርባ ሺህ አምስት መቶ ወንዶች” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:34

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

32,200

“ሠላሳ ሁለት ሺህ ሁለት መቶ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:36

ወንዶች ሁሉ በስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

35,500

“ሠላሳ አምስት ሺህ አራት መቶ ወንዶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:38

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር…. በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

62,700 ቆጠሩ

“ስድሣ ሁለት ሺህ ሰባት መቶ ቆጠሩ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:40

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

41,500 ቆጠሩ

“አርባ አንድ ሺህ አምስት መቶ ቆጠሩ”

Numbers 1:42

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

53,400 ቆጠሩ

“ሃምሳ ሶስት ሺህ አራት መቶ ቆጠሩ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:44

ወንዶች ሁሉ ከስማቸው አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠሩ

“ተቆጠሩ”የሚለው ቃል በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይሄ ሐረግ በሕዝብ ቆጠራው ወቅት ለብዙ ጊዜያት ተጠቅሷል፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡ “ወንድ ሁሉ ከስሙ አንፃር ….በየወገናቸው፤በየአባቶቻቸው ቤቶች ተቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

603,550 ወንዶች ቆጠሩ

“ስድስት መቶ ሶስት ሺህ አምስት መቶ ሃምሣ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:47

ከሌዊ ነገድ የሆኑት ግን አልተቆጠሩም

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴና አሮን ከሌዊ ወገን የሆኑትን ሰዎች አልቆጠሩም” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሌዊ ነገድ የሆኑት

በአንዳንድ ቋንቋዎች ይሄ ፍዝ ግሥ ነው፡፡አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በተለየ መንገድ ሊፃፍ ይችላል፡፡”ከሌዊ ወገን የሆኑቱ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የሌዊን ወገን አትቁጠረው

እዚህ ላይ “የሌዊ ወገን” የሚያመለክተው በሌዊ ነገድ ውስጥ ያሉትን ሰዎች ሁሉ ነው፡፡“የሌዊን ወገን አትቁጠረው” (ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:50

የማደሪያው ድንኳን የሕግ ምሥክር

የማደሪያው ድንኳን በዚህ ረዥም ሥም የሚጠራበት ምከኒያት እግዚአብሔር የምሥክሩን ሕግ ያስቀመጠው እዚያ ውስጥ በመሆኑ ነው፡፡

በእርሱ ውስጥ ያለውን ሁሉ

“በእርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የመገናኛ ድንኳኑን ነው፡፡

ሌዋውያን ማደሪያውን መሸከም ይኖርባቸዋል

ጉዞ በሚጀምሩበት ወቅት ማደሪውን የመሸከም ኃላፊነት የእነርሱ ነበር፡፡ “በምትጓዙበት ወቅት ሌዋውያን ማደሪያውን መሸከም ይኖርባቸዋል” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በማደሪያውም ዙሪያ ይስፈሩ

ይሄ ማለት ድንኳኖቻቸውን በማደሪያው ዙሪያ ይተክላሉ ማለት ነው፡፡“ድንኳኖቻቸውን በዙሪያው መትከል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 1:51

ማደሪያው በሰፈረ ጊዜ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ማደሪያው በሚያርፍበት ወቅት” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ሌላ ሰው ግን ቢቀርብ ይገደል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እንግዳ የሆነ ሰው መገደል ይኖርበታል” ወይም “ወደ ማደሪያው አካባቢ የሚመጣን እንግዳ ሰው መግደል ይኖርባችኋል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ዓርማው

ትልቅ ባንዲራ

ጭፍራዎቹ

“የጦር ክፍሎቹ”

Numbers 1:53

የማደሪያው ድንኳን የሕግ ምሥክር

ማደሪያው በዚህ ረዥም ሥም የተጠራበት ምክኒያት የእግዚአብሔር ሕግ ያለበት ምሥክሩ በውስጡ በመቀመጡ ነው፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡50 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በእሥራኤል ልጆች ላይ ቁጣዬ እንዳይወርድ

እዚህ ላይ ቁጣው በእነርሱ ላይ ስለማይወርድ እሥራኤላውያንን እንደማይቀጣቸው ነው የሚናገረው፡፡“መውረድ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ቁጣው በእነርሱ ላይ ተግባራዊ የመሆኑን ጉዳይ ነው፡፡ “በቁጣዬ የእሥራኤልን ሕዝብ እንዳልቀጣ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር በሙሴ በኩል ትዕዛዝ አስተላለፈ

እግዚአብሔር እሥራኤላውያን ሊያደርጉት ስለሚገባቸው ነገር ለሙሴ የተናገረ ሲሆን ሙሴ ደግሞ ለእሥራኤላውያን ትዕዛዙን አስተላለፈ፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 2

1 ያህዌ ለሙሴና ለአሮን እንደገና እንዲህ አለ፣ 2 “እያንዳንዱ እስራኤላዊ በየአባቶቻቸው ቤቶች በአርማው ስር በቦታው ይሰፈር፡፡ በመገናኛው ድንኳን ዙሪያ በሁሉም አቅጣጫ ይሰፍራሉ፡፡ 3 ፀሐይ በምትወጣበት፣ በመገናኛው ድንኳን በስተምስራቅ ይሁዳ በቦታው ይሰፍራል፡፡ የአሚናዳብ ልጅ ነአሶን የይሁዳ ህዝብ መሪ ነው፡፡ 4 የይሁዳ ህዝብ ቁጥር 74600 ነው፡፡ 5 የይሳኮር ጎሳ ከይሁዳ ቀጥሎ ይስፈር፡፡ የሶገር ልጅ ናትናኤል የይሳኮርን ሰራዊት ይምራ፡፡ 6 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 54400 ነው፡፡ 7 የዛብሎን ጎሳ ከይሳኮር ቀጥሎ ይስፈር፡፡ የኬሎን ልጅ ኤልያብ የኤሎንን ሰራዊት ይምራ፡፡ 8 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 57400 ነው፡፡ 9 ጠቅላላው የይሁዳ ሠራዊት ቁጥር 186400 ነው፡፡ እነርሱ በቅድሚያ ይወጣሉ፡፡ 10 በስተደቡብ አቅጣጫ የሮቤል ምድብ በስፍራው ይሆናል፡፡ የሮቤል ምድብ መሪ የሰዲዮር ልጅ ኤሊሱር ነው፡፡ 11 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 46500 ነው፡፡ 12 ስምዖን ከሮቤል ቀጥሎ ይሰፍራል፡፡ የስምዖን ህዝብ መሪ የሱሪሰዳይ ልጅ ስለሚኤል ነው፡፡ 13 በእርሱ ምድብ የሚገኘው የሰራዊት ቁጥር 59, 300 ነው፡፡ 14 የጋድ ጎሳ ይቀጥላል፡፡ የጋድ ህዝብ መሪ የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ ነው፡፡ 15 በእርሱ ምድብ የሚገኘው የሰራዊት ቁጥር 45650 ነው፡፡ 16 በሮቤል ምድብ የሚገኙት በክፍላቸው መሠረት 151450 ናቸው፡፡ እነርሱ ቀጥለው ይወጣሉ፡፡ 17 ቀጥሎ፣ የመገናኛው ድንኳን ሌዋውያንን ከሁሉም ምድብተኞች መሃል አድርጎ ከሰፈር ይወጣል፡፡ ወደ ሰፈር በገቡበት ስርዓት ከሰፈር ይውጡ፡፡ እያንዳንዱ ሰው በዐርማው ስር በስፍራው ይሁን፡፡ 18 የኤፍሬም ሰፈር ክፍሎች በስፍራቸው ይሁኑ፡፡ የኤፍሬም ህዝብ መሪ የዓሚሁድ ልጅ ኤሊሳማ ነው፡፡ 19 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 40500 ነው፡፡ 20 ከእነርሱ የሚቀጥለው የምናሴ ጎሳ ነው፡፡ የምናሴ መሪ የፍርዱሱር ልጅ ገማልኤል ነው፡፡ 21 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 32200 ነው፡፡ 22 ቀጣይ የሚሆነው የብንያም ጎሳ ነው፡፡ የብንያም መሪ የጋዴዮን ልጅ አቢዳን ነው፡፡ 23 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 35400 ነው፡፡ 24 በኤፍሬም ምድብ የሚኙት በክፍላቸው መሰረት 108100 ናቸው፡፡ እነርሱ ሶስተኛ ሆነው ይወጣሉ፡፡ 25 በሰሜን የዳን ሰፈር ምድብተኞች ይሰፍራሉ፡፡ የዳን ህዝብ መሪ የአሚሳዓይ ልጅ አብዔዘር ነው፡፡ 26 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 62700 ነው፡፡ 27 የአሴር ጎሳ ህዝብ ሰፈር ከዳን ቀጥሎ ነው፡፡ የአሴር መሪ የኤክራን ልጅ ፋግኤል ነው፡፡ 28 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 41500 ነው፡፡ 29 ቀጣዩ የንፍታሌም ጎሳ ነው፡፡ የንፍታሌም መሪ የዔናን ልጅ አኪሬ ነው፡፡ 30 በእርሱ ክፍል የሰራዊቱ ቁጥር 53400 ነው፡፡ 31 ከዳን ጋር በሰፈር የሚገኙት ቁጥራቸው 157600 ነው፡፡ እነርሱ በዐርማቸው ስር ከሰፈር በመጨረሻ ይወጣሉ፡፡” 32 በየቤተሰባቸው የተቆጠሩት እስራኤላውያን እነዚህ ናቸው፡፡ በየክፍሎቻቸው በሰፈሮቻቸው የተቆጠሩት በጠቅላላ 603550 ናቸው፡፡ 33 ነገር ግን ሙሴና አሮን በእስራኤል ሕዝብ መሀል ሌዋውያንን አልቆጠሩም፡፡ ይህም ያህዌ ሙሴን ባዘዘው መሠረት ነበር፡፡ 34 የእስራኤል ሕዝብ ያህዌ ሙሴን ያዘዘውን ነገር ሁሉ አደረጉ፡፡ በየአርማቸው ስር ሰፈሩ፡፡ በአባቶቻቸው ቤቶች መሠረት በየነገዳቸው ከሰፈር ወጡ፡፡



Numbers 2:1

በየአባቶቻቸው ቤቶች ምልክት አንፃር

“የአባቶች ቤቶች ምልክቶች” የሚባሉት ነገዶች በአራት ትላልቅ ቡድኖች የሚከፋፈሉበት ሁኔታ ነው፡፡እያንዳንዳቸው የተከፈሉት የአባቶች ቤቶች በአንድ ላይ መስፈር ነበረባቸው፡፡የአባቶች ቤቶች ወይም ነገዶች የሚለዩት በሚይዙት ዓርማ ነው፡፡

በየአባቶቻቸው በቶች ምልክቶች አንፃር

እያንዳንዱ ዘመድ አዝማድ ከዓርማቸው አንፃር ለእነርሱ መቀመጫ እንዲሆን የተመደበላቸው የመሥፈሪያ ቦታ ነበራቸው፡፡

ምልክቶች

ምልክት ትልቅ ባንዲራ ነው፡፡

Numbers 2:3

በዓላማቸው ምልክት ሥር

“የአባቶች ቤቶች ምልክቶች” ማለት ነገዶች በትላልቅ ቡድኖች የሚከፋፈሉበት ነው፡፡እያንዳንዱ ነገድ በአንድነት ላይ እንዲሰፍር የሚታዘዝ ሲሆን እነርሱን የሚወክል ዓርማ ነበራቸው፡፡በኦሪት ዘኀልቁ 2፡2 ላይ የአባቶች ቤቶች ምልክቶች የሚለውን እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የአሚናዳብ ልጅ ነአሶን

በዘኁልቁ 1፡7 ላይ ይሄንን እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

74,600

“ሰባ አራት ሺህ ስድስት መቶ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:5

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የኬሎን ልጅ ኤልያብ

የዚህን ሰው ስም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

57,400

“ሃምሣ ሰባት ሺህ አራት መቶ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡“57,400” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:7

የኬሎን ልጅ ኤልያብ

የዚህን ሰው ስም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

57,400

“ሃምሣ ሰባት ሺህ አራት መቶ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡“57,400” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:9

የተቆጠሩት ሁሉ…186,400

“ቁጥሩ በአጠቃላይ አንድ መቶ ሰማንያ ስድሰት ሺህ አራት መቶ ነው፡፡”ይሄ ቁጥር በየአባቶቻቸው በቶች ምልክት ሥር የሰፈሩትን የይሁዳ ነገድ ሰዎች የሚያካትት ነው፡፡ “በይሁዳ ዓርማ ሥር የሰፈሩት ሰዎች ቁጥር 186,400 ነው፡፡”

የይሁዳ ሠፈር

ይሄ የሚያመለክተው ከመገናኛ ድንኳኑ በስተ ምሥራቅ በኩል የሚሰፍሩትን የይሁዳ፤የይሳኮርና የዛብሎንን ነገዶች ነው፡፡

አስቀድመው ይጓዛሉ

ይሄ ማለት እሥራኤላውያን ከሠፈራቸው መንቀሳቀስ በሚጀምሩበት ወቅት ሌሎች ነገዶች ከመንቀሳቀሳቸው በፊት የይሁዳ ነገድ ከፊታቸው በመቅደም መጓዝ ይጀምራል ማለት ነው፡፡“በጉዞ ወቅት የይሁዳ ነገድ ቀዳሚ ይሆናል፡፡” ወይም “እሥራኤላውያን የሰፈሩበትን ቦታ በሚለቁበት ወቅት እነዚያ ነገዶች የመጀመሪያዎቹ ይሆናሉ” (ቁጥሮች የሚለውንና በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በዓላማቸው ምልክት ሥር

“በየአባቶቻቸው በቶች ምልክት”ማለት አራት ነገዶች በትላልቅ ቡድኖች የሚከፋፈሉበት ሁኔታ ነው፡፡እያእንዳንዱ ነገድ በአንድ ላይ እንዲሰፍር የሚታዘዝ ሲሆን እነርሱን የሚወክል ዓርማ ነበራቸው፡፡በኦሪት ዘኀልቁ 2፡2 ላይ በየአባቶቻቸው በቶች ምልክት የሚለውን እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 2:10

የሰዲዮር ልጅ ኤሊሱር

የዚህን ሰው ሥም በዘኁልቁ 1፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

46,500

“አርባ ስድስት ሺህ አምስት መቶ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎችን ቁጥር ነው፡፡“46,500”(ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:12

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የራጉኤል ልጅ ሰለሚኤል

የዚህን ሰው ሥም በዘኁልቁ 1፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

59,300

“ሃምሳ ዘጠኝ ሺህ ሶስት መቶ”ይሄ የሚያመለክተው የሰዎችን ቁጥር ነው፡፡ “59,300” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:14

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

45,650

“አርባ አምስት ሺህ ስድስት መቶ ሃምሣ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎችን ቁጥር ነው፡፡ “45,650” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:16

የተቆጠሩት ሰዎች በአጠቃላይ … 151,450 ናቸው

“የተቆጠሩት ሰዎች በአጠቃላይ … አንድ መቶ ሃምሣ አንድ ሺህ አራት መቶ ሃምሣ ናቸው” ይሄ ቁጥር በሮቤል የአባቶቻቸው በቶች ዓርማ ሥር የሰፈሩትን ወንዶች ሁሉ የሚያካትት ቁጥር ነው፡፡“በተከፋፈሉበት ክፍል መሠረት በሮቤል የአባቶቻቸው በቶች ምልክት ሥር የሰፈሩት ወንዶች ሁሉ ቁጥር 151,450 ነው፡፡” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱም ቀጥለው ይጓዛሉ

ይሄ ማለት እሥራኤላውያን ሠፈራቸውን ለቀው መጓዝ በሚጀምሩበት ወቅት የሮቤል ሠፈር ከይሁዳ በመቀጠል ጉዞውን ይቀጥላል ማለት ነው፡፡“በጉዞ ወቅት የሮቤል ሠፈር ሁለተኛ በመሆን ጉዞውን ይጀምራል”ወይም “እሥራኤላውያን ሠፈሩን ለቅቀው በሚሄዱበት ወቅት እነዚያ ነገዶች በሁለተኛ ረድፍነት መጓዝ ይቀጥላሉ”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:17

የመገናኛው ድንኳን በሰፈሮቹ መካከል ይጓዛል

ይሄ ማለት በሚጓዙበት ወቅት የመገናኛው ድንኳን ሌዋውያን ተሸክመውት በነገዶቹ መካከል መጓዝ ይኖርበታል ማለት ነው፡፡

እነርሱ መጓዝ ይኖርባቸዋል

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አሥራ ሁለቱን ነገዶች ነው፡፡

በዓርማው

እያንዳንዱ ግለሰብ የራሱ የሆነ ምልክት ወይም ዓርማ ሊኖረው አይችልም፡፡ይሄ የሚያመለክተው የነገዱን ምልክት ነው፡፡ “በነገዱ ዓርማ” (ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:18

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በየአባቶቻቸው በቶች ዓርማ ሥር

“በየአባቶቻቸው በቶች ዓርማ ሥር” ማለት ነገዶቹ የተከፋፈሉባቸው አራት ትላልቅ ቡድኖች ናቸው”እያንዳንዱ ነገድ ከዓርማው አንፃር አንድ ላይ እንዲሰፍር ይታዘዝ ነበር“የአባቶች ቤቶች የሚወከሉት በዓርማ ነው፡፡በኦሪት ዘኁልቁ 2፡2 ላይ “ዓርማ” የሚለውን እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

40,500

“አርባ ሺህ አምስት መቶ”ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡ “40,500” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:20

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ከእነርሱ በመቀጠል

ይህ ማለት ከኤፍሬም ነገድ በመቀጠል የምናሴ ነገድ ይከተላል ማለት ነው፡፡

32,200

“ሰላሣ ሁለት ሺህ ሁለት መቶ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡“32,200 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:22

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የጋዴዮን ልጅ አቢዳን

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

35,400

“ሰላሣ አምስት ሺህ አራት መቶ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡“35,400 ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:24

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የተቆጠሩት ሁሉ 108,100 ነበሩ

“የተቆጠሩት አንድ መቶ ስምንት ሺህ አንድ መቶ ነበሩ” ”ይሄ ቁጥር በኤፍሬም የአባቶች ቤቶች ዓርማ ሥር የሰፈሩትን የነገድ ሰዎች የሚያካትት ነው፡፡ “በኤፍሬም ዓርማ ሥር የሰፈሩት ሰዎች ቁጥር 108,100 ነበር፡፡” (ቁጥሮች የሚለውንና በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱም ሶስተኛ ሆነው ይጓዛሉ

ይሄ ማለት እሥራኤላውያን ከሰፈራቸው ሲንቀሳቀሱ የኤፍሬም ነገድ ከይሁዳና ከሮቤል በመቀጠል ጉዞውን ይጀምራል ማለት ነው፡፡“ጉዞ በሚጀመርበት ወቅት የኤፍሬም ሠፈር ሶስተኛ ሆኖ ጉዞውን ይቀጥላል” ወይም “እሥራኤላውያን የሰፈሩበትን ሥፍራ በሚለቅቁበት ወቅት እነዚያ ነገዶች ቀጥለው ይለቅቃሉ” (ተከታታይ ቁጥሮችንና በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:25

የዳን ሠፈር ሠራዊቶች

ይሄ የሚያመለክተው በዳን ነገድ ምልክት ሥር የሚገኙትን የዳን፤የአሴርና የንፍታሌምን ሠራዊቶች ነው፡፡ “በዳን ምልክት ሥር የሚሰፍሩ ሠራዊቶች” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የአሚሳዳይ ልጅ አኪኤዘር

የዚህን ሰው ሥም በዘኁልቁ 1፡12 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

62,700

“ስድሳ ሁለት ሺህ ሰባት መቶ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡“62,700 ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:27

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የኤክራን ልጅ ፋግኤል

ይህንን ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

41,500

“አርባ አንድ ሺህ አምስት መቶ” ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡“41,500” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:29

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡ (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

የዔናን ልጅ አኪሬ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

53,400

“ሃምሣ ሶስት ሺህ አራት መቶ”ይሄ የሚያመለክተው የሰዎችን ቁጥር ነው፡፡“53,400” (ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:31

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር እያንዳንዱ ነገድና ሠራዊቱ የት ሥፍራ ላይ እንደሚሰፍሩ ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የተቆጠሩት ሰዎች ሁሉ….157,600

“የተቆጠሩት ሁሉ …አንድ መቶ ሃምሣ ሰባት ሺህ ስድስት መቶ” ”ይሄ ቁጥር በዳን የአባቶች ቤቶች ምልክት ሥር የሰፈሩትን የነገድ ሰዎች የሚያካትት ነው፡፡“በዳን ምልክት ሥር የሰፈሩት የሰዎቸ ቁጥር 157,600” (ቁጥሮች የሚለውንና በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:32

የተቆጠሩት ሁሉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴና አሮን ሁሉንም ቆጠሯቸው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱ በየሠራዊታቸው

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡

603,550 ናቸው

“ስድስት መቶ ሶስት ሺህ አምስት መቶ ሃምሣ ናቸው፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 2:34

ከየሠፈሮቻቸው ወጡ

ይሄ የሚያመለክተው ወደሌላ ሥፍራ መቼ መንቀሳቀስ እንዳለባቸው ነው፡፡“መጓዝ ሲጀምሩ ከሠፈራቸው ይወጡ ነበር” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 3

1 ያህዌ በሲና ተራራ ከሙሴ ጋር በተነጋገረበት ጊዜ የአሮንና የሙሴ ትውልዶች ታሪክ ይህ ነበር፡፡ 2 የአሮን ልጆች ስሞቻቸው የበኩር ልጁ ናዳብ፣ እንዲሁም አብዩድ፣ አልዓዛር እና ኢታምር ነበሩ፡፡ 3 የአሮን ልጆች ስሞች እነዚህ ናቸው፣ እነዚህ የተቀቡ ካህናትና እንደ ካህናት ሊያገለግሉ የተሾሙ ነበሩ፡፡ 4 ነገር ግን ናዳብ እና አብዩድ በሲና ምድረበዳ ተቀባይነት የሌለው እሳት ለእርሱ ሲሰዉ በያህዌ ፊት ወድቀው ሞቱ፡፡ ናዳብና አብዩድ ልጅ አልነበራቸውም፣ ስለዚህም አልዓዛርና ኢታምር ብቻ ከአባታቸው ከአሮን ጋር ካህናት ሆነው አገለገሉ፡፡ 5 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 6 “የሌዊን ጎሳ ይረዱት ዘንድ ወደ ካህኑ ወደ አሮን አምጣቸው፡፡ 7 በአሮንና በመላው ማህበሩ ስም በመገናኛው ድንኳን ፊት አገልግሎት ይስጡ፡፡ በቤተመቅደሱ ውስጥ ያገልግሉ፡፡ 8 በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ላሉ ነገሮች ሁሉ ጥንቃቄ ያድርጉ፣ እንዲሁም የእስራኤል ጎሳዎች የቤተ መቅደሱን አገልግሎት እንድፈጽም ይርዱ፡፡ 9 ሌዋውያኑን ለአሮንና ለልጆቹ ስጥ፡፡ እነርሱ የእስራኤልን ሕዝብ እንዲያገለግል ሙሉ ለሙሉ የተሰጡ ናቸው፡፡ 10 አሮንንና ልጆቹን ካህን አድርገህ ሹማቸው፣ ነገር ግን ማናቸውም ባዕድ ወደ ቤተ መቅደሱ ቢቀርብ ይገደል፡፡” 11 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 12 “እነሆ፣ እኔ ከእስራኤል ህዝብ መሃል ሌዋውያንን መረጥኩ፡፡ ከእስራኤል ሕዝብ መሃል በኩር የሆነውን ወንድ ሁሉ ከመውሰድ ፈንታ ይህን አድርጌያለሁ፡፡ ሌዋዊያን የእኔ ናቸው፡፡ 13 ማናቸውም በኩር የእኔ ነው፡፡ በግብጽ ምድር በኩሩን ሁሉ በመታሁ ዕለት፣ በእስራኤል በኩር ሆኖ የተወለደውን የሰውንም ሆነ የእንስሳትን በኩር ሁሉ ለራሴ ለየሁ፡፡ እነርሱ የእኔ ናቸው፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡” 14 በሲና ምድረበዳ ያህዌ ሙሴን ተናገረው፡፡ እንዲህም አለው፣ 15 “በእያንዳንዱ ቤተሰብ፣ በአባቶቻቸው ቤቶች የሌዊን ትውልዶች ቁጠር፡፡ አንድ ወር እና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያለውን ወንድ ሁሉ ቁጠር፡፡” 16 ሙሴ እንዲያደርግ በታዘዘው መሠረት የያህዌን ቃል ሰምቶ ቆጠራቸው፡፡ 17 የሌዊ ልጆች ስም፣ ጌድሶን፣ ቀዓትና ሜራሪ ናቸው፡፡ 18 ከጌድሶን ልጆች የመጡ ነገዶች ሎቢኒ እና ሰሜኢ ናቸው፡፡ 19 ከቀዓት ልጆች የመጡ ነገዶች፣ አንበረም፣ ይስዓር፣ኬብሮን እና ዑዝኤል ናቸው፡፡ 20 ከሜራሪ ልጆች የመጡ ነገዶች፣ ሞሖሊና ሙሴ ናቸው፡፡ በነገድ የተዘረዘሩ የሌዋውያን ነገዶች እነዚህ ናቸው፡፡ 21 የሊቤናና የሰሜአ ነገዶች የመጡት ከጌርሶን ነው፡፡ እነዚህ የጌርሶን ነገዶች ናቸው፡፡ 22 አንድ ወር ከሞላው አንስቶ ከዚያ በላይ ዕድሜ ያለው ወንድ ሁሉ ተቆጥሮ ነበር፣ በጠቅላላው 7500 ነበሩ፡፡ 23 የጌርሶን ነገዶች ከቤተመቅደሱ ምዕራብ አቅጣጫ ይስፈሩ፡፡ 24 የጌርሶንን ትውልዶች የላኤለ ልጅ ኤሊሳፍ ይምራ፡፡ 25 የጌርሶን ቤተሰብ የመገናኛው ድንኳን ጨምሮ የማደሪያውን ድንኳን ኃላፊነት ይውሰድ፡፡ እነርሱ ለድንኳኑ፣ ለመደረቢያዎቹና ለመገናኛው ድንኳን መግቢያ ሆኖ ለሚያገለግለው መጋረጃ ጥንቃቄ ያደርጉ፡፡ 26 ለአደባባዩ ጌጦች ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው፣ በአደባባይ መግቢያ ላይ ለሚገኘው መጋረጃ፣ ቅዱሱን ስፍራና መሰዊያውን የሚከበውን አደባባይ ይጠብቁ፡፡ የመገናኛው ድንኳን ገመዶች እና በውስጡ የሚገኘውን ነገር ሁሉ ይጠብቁ፡፡ 27 ከቀዓት የመጡት ነገዶች እነዚህ ናቸው የአንበረማውያን ነገድ የይሰዓራውያን ነገድ፣ የኬብሮናውያን ነገድ፣ እና የዑዝኤላውያን ነገድ ናቸው፡፡ እነዚህ ነገዶች የቀዓት ወገኖች ናቸው፡፡ 28 አንድ ወር እና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላቸው 8600 ወንዶች የያህዌ የሆኑ ነገሮችን ለመጠበቅ ተቆጠሩ፡፡ 29 የቀዓት ቤተሰብ ትውልዶች ከቤተ መቅደሱ በስተደቡብ አቅጣጫ ይስፈሩ፡፡ 30 የዑዝኤል ልጅ ኤሊሳፈን የቀዓታዊያንን ነገድ ይምራ፡፡ 31 እነርሱ ታቦቱን፣ ጠረጴዛውን፣ የመቅረዝ ማስቀመጫውን፣ መሰዊያዎቹን፣ ለአገልግሎታቸው የሚጠቀሙባቸውን ቅዱሳን ዕቃዎች፣ መጋረጃውን፣ እና በዚያ ዙሪያ ያለውን ስራ ሁሉ ይንከባከቡ፡፡ 32 የካህኑ የአሮን ልጅ አልዓዛር ሌዋውያንን የሚመሩትን ሰዎች ይምሩ፡፡ እርሱ ቅዱሱን ስፍራ የሚንከባከቡትን ሰዎች ይቆጣጠር፡፡ 33 ሁለቱ ነገዶች ኮሜራሪ ነገድ የመጡ ናቸው፡ እነዚህም የሞሖላውያን ነገድ እና የሙሳያውያን ነገድ ናቸው፡፡ እነዚህ ነገዶች የመጡት ከሜራሪ ነው፡፡ 34 አንድ ወርና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላቸው 6200 ወንዶች ተቆጠሩ፡፡ 35 የሜራሪን ነገድ የአቢካኤል ልጅ ሲሪኤል ይምራ፡፡ 36 እነርሱ የቤተመቅደሱን ጣውላዎች፣ መቀርቀሪያዎች፣ ምሰሶዎች፣ መሰረቶች፣ ሁሉንም መገልገያዎች፣ እና ከእነርሱ ጋር የተያያዙ ነገሮች ሁሉ፣ 37 መቅደሱ ዙሪያ የሚገኙ ምሰሶዎችና ቋሚዎችን ጨምሮ፣ ከማስገቢያዎቻቸው፣ ችካሎችና ገመዶች ጋር ይጠብቁ፡፡ 38 ሙሴ፣ አሮን እና ልጆቹ ከመገናኛው ድንኳን ፊት ለፊት፣ በፀሀይ ማውጫ ከቤተ መቅደሱ በስተ ምስራቅ ይስፈሩ፡፡ እነርሱ በቅድስተ ቅዱሳን ለሚከናወኑ ተግባራት እና ለእስራኤል ህዝብ ግዴታዎች ሀላፊነት አለባቸው፡፡ ማንኛውም ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ የሚቀርብ ባዕድ ይገደል፡፡ 39 ሙሴና አሮን ያህዌ እንዳዘዘው በሌዊ ነገዶች ውስጥ የሚገኙትን አንድ ወርና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላቸውን ወንዶች ሁሉ ቆጠሩ፡፡ ሃያ ሁለት ሺህ ወንዶችን ቆጠሩ፡፡ 40 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “አንድ ወር ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላቸውን በኩር የሆኑ የእስራኤል ወንዶች ቁጠር፡፡ ስሞቻቸውን ጻፍ፡፡ 41 በእስራኤል ህዝብ በኩር ምትክ ሌዋውያንን ለእኔ ውሰድ፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ እንደዚሁም የሌዋውያንን ቀንድ ከብቶች፣ በመጀመሪያ በሚወለዱ የእስራኤላውያን የቀንድ ከብቶች ምትክ ውሰድ፡፡” 42 ያህዌ እንዳዘዘው ሙሴ የእስራኤልን ሰዎች በኩር በሙሉ ቆጠረ፡፡ 43 ዕድሜያቸው አንድ ወርና ከዚያ በላይ የሆኑትን በኩር ወንዶች ሁሉ በስም ቆጠረ፡፡ 22273 ወንዶችን ቆጠረ፡፡ 44 እንደገና፣ ያህዌ ሙሴን ተናገረው፡፡ እንዲህም አለው፣ 45 “በእስራኤል ህዝብ በኩር ሁሉ ምትክ ሌዋውያንን ውሰድ፡፡ በህዝቡ የቀንድ ከብት ምትክ የሌዋውያንን ቀንድ ከብት ውሰድ፡፡ ሌዋውያን የእኔ ናቸው፡፡ እኔ ያህዌ ነኝ፡፡ 46 ከሌዋውያን ቁጥር በላይ የሆኑትን 273 የእስራኤል በኩሮች ለመዋጀት ለእያንዳንዳቸው አምስት ሰቅሎች ተቀበል፡፡ 47 የቅድስተ ቅዱሳኑን ሰቅል እንደ መደበኛ ክብደት ተጠቀም፡፡ (አንድ ሰቅል አምሳ አምስት ግራም ነው) 48 ያገኘኸውን የመዋጆ ዋጋ ለአሮንና ለልጆቹ ስጥ፡፡” 49 ስለዚህም ሙሴ በሌዋውያን ከተዋጁት በላይ ቁጥራቸው ያለፈውን መዋጃ ክፍያ ሰበሰበ፡፡ 50 ሙሴ ከእስራኤል ሕዝብ በኩሮች ገንዘብ ሰበሰበ፡፡ በቤተ መቅደሱ ሚዛን መዝኖ 1365 ሰቅሎች ሰበሰበ፡፡ 51 ሙሴ ለአሮንና ለልጆቹ የመዋጃውን ገንዘብ ሰጣቸው፡፡ ሙሴ ያህዌ እንዲያደርግ የተናገረውን ሁሉ አደረገ፣ ያህዌ እንዳዘዘው አደረገ፡፡



Numbers 3:1

አሁን

እዚሀ ላይ ፀሐፊው “አሁን” የሚለውን ቃል የተጠቀመው አዲስ የታሪክ ዘገባን መናገር ሲጀምር ነው፡፡

በኩሩ ናዳብ

“ናዳብ በኩር ነበር፡፡

ናዳብ…አብድዩ..ኢታምር

እነዚህ የሰው ሥሞች ናቸው፡፡(ስሞችን እንዴት መተርጎም እንደሚገባ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:3

በክህነት የተቀቡና የተቀደሱት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴ የቀባቸውና የቀደሳቸው” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ናዳብ…አብድዩ..ኢታምር

የእዚህን ሰዎች ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 3፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በእግዚአብሔር ፊት ሞቱ

“ሞቱ”የሚለው ቃል በድንገት ሞቱ ለማለት ነው፡፡ “በእግዚአብሔር ፊት ድንገት ሞቱ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ፊት

ይሄ የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን መገኘት ነው፡፡ማለትም የሚከናወነውን ነገር ሁሉ እግዚአብሔር ይመለከት ነበር ለማለት ነው፡፡“በእግዚአብሔር ህልውና ፊት” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ተቀባይነት የሌለውን እሣት አቀረቡ

እዚህ ላይ “እሣት”የሚለው ቃል “የሚቃጠል መሥዋዕት”የሚለውን ሃሣብ ለመግለፅ የዋለ ቃል ነው፡፡“እግዚአብሔር ያልተቀበለውን የሚቃጠል መሥዋዕት አቀረቡ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:5

የሌዊን ነገድ አቅርብ

እዚህ ላይ “ነገድ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የነገዱን ሰዎች ነው፡፡“የሌዊን ነገድ ሰዎች አቅርብ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:7

በውክልና

ይሄ ማለት በእነርሱ ምትክ ነገሮችን ተግባራዊ ማድረግ ማለት ነው፡፡

የእሥራኤልን ነገዶች እርዱ

እዚህ ላይ “የእሥራኤል ነገዶች”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡“የእሥራኤልን ሕዝብ እርዱ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የመገናኛውን ድንኳን አገልግሎት ሥራ ማካሄድ ይችሉ ዘንድ የእሥራኤልን ነገዶች መርዳት ይኖርባቸዋል

“ማካሄድ”የሚለው ቃል ትርጉም “ማገልገል” ማለት ነው፡፡“በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ አገልግሎትን በመሥጠት የእሥራኤልን ነገዶች ሊያግዟቸው ይገባል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የመገናኛ ድንኳን አገልግሎት

“የመገናኛ ድንኳን ሥራ”

Numbers 3:9

አንተ መስጠት ይኖርብሃል

“አንተ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴን ነው፡፡

በሙላት ተሰጥቷቸዋል

ይሄ በድጊጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሉ በሙሉ ሰጥቻቸዋለሁ፡፡”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ሌላ ሰውም ቢቀርብ ይገደል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እዚያ አጠገብ የሚደርስ ማንኛውንም እንግዳ ሰው መግደል አለባችሁ” ወይም “እዚያ አካባቢ የሚደርስ ሌላ ሰው ሞት ይጠብቀዋል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እዚያ አጠገብ የሚመጣ ሌላ ሰው

የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ፍቺ ግልፅ ሊደረግ ይችላል፡፡“ማንኛውም ወደ መገናኛ ድንኳኑ የሚቀርብ እንግዳ ሰው” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:11

ተመልከት

“አዳምጥ”ወይም “ለምነግርህ ነገር ትኩረት ስጥ”

ሌዋውያንን ወስጄአለሁ

“ሌዋውያንን መርጫለሁ”

Numbers 3:14

ትውልዳቸውን ቁጠር

እግዚአብሔር ወንድ የሆኑ ትውልዶችን እንዲቆጥር ሙሴን እያዘዘው ነው፡፡“ወንድ የሆኑትን ቁጠር” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔር ቃል በመከተል፤እርሱ ባዘዘው መሠረት

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን አንድ ላይ በመቀናጀት የቀረቡት እግዚአብሔርን ስለመታዘዙ አፅንዖት ለመስጠት ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:17

አጠቃላይ መረጃ

ይሄ የሌዊ ትውልዶች የሥም ዝርዝር ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ሲወርድ ሲዋረድ ከመጡበት ወገን አንፃር

እዚህ ላይ ፀሐፊው “ሲወርድ ሲዋረድ”ሲል አገላለለፁ ልክ “እየመጡ” እንደሆነ ዓይነት ይመስላል፡፡“ሲወርድ ሲዋረድ የሚመጡ ነገዶች” “የጌድሶን ትውልድ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:21

ከጌድሶን ትውልድ ሲወርድ ሲዋረድ የመጡ

እዚህ ላይ ፀሐፊው በእንቅስቃሴ ላይ ያሉ ይመስል የሚወርዱ ብሎ ይናገራል፡፡“እየተንቀሳቀሰ የሚመጣ ይመስል” ወይም “ከጌድሶን ወገን ትውልድ ሲወርድ ሲዋረድ የመጡ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሎቤናውያን…ሰሜአውያን…ጌድሶናውያን

“ሎቤናውያን” እና “ሰሜአውያን”በየትውልዳቸው ከአባቶቻቸው ቤቶች ሥም አንፃር የሚጠሩበት ሥም ነው፡፡ “ጌድሶናውያን” ከጌድሶን ትውልድ የመጡ ሰዎች ሥም ነው፡፡((ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ))

ከአንድ ወር ጀምሮ ከዚያ በላይ ያለው ወንድ ሁሉ ተቆጠረ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴ ዕድሜያቸው ከአንድ ወር ጀምሮ ያሉትን ወንዶች ሁሉ ቆጠረ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

7,500

“ሰባ አምስት መቶ”ወይም “ሰባት ሺህ አምስት መቶ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:24

ኤሊሳፍ…ዳኤል

እነዚህ የሰው ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የመገናኛ ድንኳን ደጃፍ መጋረጃ

“በመገናኛ ድንኳኑ ደጃፍ ያለው መጋረጃ”

በማደሪያውና በመሠዊያው ዙሪያ ያለው አደባባይ

“ማለትም ማደሪያውንና መሠዊያውን የሚከብበው አደባባይ”

Numbers 3:27

አጠቃላይ መረጃ

እነዚህ ከቀአት ወገን የሆኑ የነገዶች ሥም ዝርዝር ነው፡፡ (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ቀአት

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

86,000 ወንዶች ተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴ 86,000 ሺህ ወንዶችን ቆጠረ”

86,000 ወንዶች

“ሰማንያ ስድስት ሺህ”(ኦሪት ዘኁልቁን ይመልከቱ)

ከአንድ ወር ጀምሮ ከዚያም በላይ

“አንድ ወር ከሞላው ጀምሮ ከዚያ በላይ”

Numbers 3:30

አጠቃላይ መረጃ

እነዚህ ቁጥሮች ከቀአት ዝርያ ስለመጡት ነገዶች መረጃን ይሰጠናል፡፡“(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

በአገልግሎት ወቅት የሚጠቀሙባቸው የተቀደሱ ዕቃዎች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ካህናት ለአገልግሎታቸው የሚጠቀሙባቸው የተቀደሱ ዕቃዎች”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:33

እነዚህ ከሜራሪ ዝርያ የመጡ የነገዶች ሥም ዝርዝር ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

እነዚህ ከሜራሪ ዝርያ የመጡ የነገዶች ሥም ዝርዝር ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

6,200 ወንዶች ተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይቸላል፡፡“ሙሴ 6,200 ወንዶችን ቆጠረ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

6,200 ወንዶች

“ስድስት ሺህ ሁለት መቶ ወንዶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:36

ክፈፎች

እነዚህ ትናንሽ እንጨቶችን አንድ ላይ በማድረግ የግድግዳዎች ወይም የበሮች የተወሰኑ ክፍሎች የሚሰሩበት ነው፡፡

ፍርግርጎች

እነዚህ ለሕንፃው ጥንካሬን የሚሰጡ ደጋፊ ርብራቦች ናቸው፡፡

ምሰሶ

ምሰሶ ከእንጨት የተሰራ ሆኖ ወደላይ ቀጥ ብሎ የሚቆምና ቤትን ለመደገፍ ጥቅም ላይ የሚውል ነገር ነው፡፡

መሠረቶች

መሰረቶች ምሰሶዎች በቦታቸው ላይ ፀንተው እንዲቆሙ የሚያደርጉ ነገሮች ናቸው፡፡

የመሥሪያ ቁሣቁሶች

ይሄ ማለት ርብራቦቹን፤ማቆሚያዎቹንና መሠረቶቹን ለማገናኘት የሚጠቅሙ ቁሣቁሶች ሁሉ ናቸው፡፡

ካስማዎቹ

እዚህ ላይ “ካስማዎቹ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ምሰሶዎቹንና አውታሮቹን ነው፡፡

Numbers 3:38

የእርሱ ልጆች

እዚህ ላይ “የእርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አሮንን ነው፡፡

በስተ ፀሐይ መውጫ

ይሄ የመገናኛው ድንኳን የምሥራቅ አቅጣጫ ነው፡፡“ፀሐይ በሚወጣበት ምሥራቅ አቅጣጫ” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ሥራው ይፈፀም ዘንድ

“መፈፀም”የሚለው አሕፅሮተ ሥም ሲሆን እንደ ሥም ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሥራዎችን ማከናወን” (አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

ልዩ ሰውም ቢቀርብ ይገደል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ወደ መቅደሱ የሚጠጋውን እንግዳ ሰው ግደሉ”ወይም “ወደ መቅደሱ የሚጠጋ ማንኛውም ልዩ ሰው መገደል ይኖርበታል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ሃያ ሁለት ሺህ ሰዎች

“22,000 ሰዎች” ወይም ”22,000 ወንዶች“ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:40

የሌዋውያን እንስሳት

ይሄ የሚያመለክተው የሌዋውያንን እንስሳት ነው፡፡“የሌዋውያንን ከብቶች ሁሉ መውሰድ ይኖርብሃል፡፡”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:42

በኩር የሆኑትን ሰዎች

“በኩር የሆኑትን ወንዶች ሁሉ”

22,273 ወንዶች

“ሃያ ሁለት ሺህ ሁለት መቶ ሰባ ሶስት” ወንዶች“(ቀጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 3:46

ለመዋጀት ሲባል

“መዋጀት”የሚለው ስም(ሰዋሰው) “መዋጀት”በሚለው ግሥ ሊተረጎም ይችላል፡፡“መዋጀት”(አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

273 የበኩር ልጆች

“ሁለት መቶ ሰባ ሶስት የበኩር ልጆች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል የበኩር ልጆች

“የእሥራኤል ወንድ የበኩር ልጆች”

አምስት ሰቅል

አንድ ሰቅል በግምት ከ11 ግራም ጋር የሚሰተካከል ነው፡፡“55 ግራም አካባቢ”(የመፅሐፍ ቅዱስ ሚዛንና የመፅሐፍ ቅዱስ ገንዘብ የሚለውን ይመልከቱ)

የሌዋውያንን ቁጥር የሚበልጡትን

ይሄ ማለት ከአጠቃላይ የሌዋውያን ቁጥር ይልቅ በእሥራኤል ውስጥ በሚገኙ ለሎች ነገዶች ውስጥ 273 ወንዶች አሉ ማለት ነው፡፡

እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን ትወስዳለህ

ይሄ ማለት የሰቅሉ ሚዛን ቤተመቅደስ ውስጥ ከሚገኙት ጋር ተመሳሳይነት ሊኖረው ይገባል ማለት ነው፡፡“ለሰቅሉ ሚዛን መለኪያ የምታደርገው ቤተመቅደሱ ውስጥ ካለው ጋር በማስተያየት ነው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ሃያ አቦሊ

“ሃያ አቦሊ”አንድ አቦሊ ከ .57 ኪሎ ግራም ጋር ተመጣጣኝነት ያለው ነው፡፡(ቁጥሮች የሚለውንና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

የመቤዣውን ገንዘብ የከፈልከው

እዚህ ላይ“ገንዘብ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴ የሰበሰባቸውን ሰቅሎች ነው፡፡“ለመቤዣቸው የሰበሰብከው ገንዘብ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ከ..የሚቤዡትን

ይሄ “መቤዠት”የሚለው ስም(ሰዋሰው) “ተቤዠ”በሚል ሥም ሊተረጎም ይችላል፡፡“መቤዠት”(አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

1,365 ሰቅሎች

“አንድ ሺህ ሶስት መቶ ስድሣ አምስት ሰቅሎች”አንድ ሰቅል 11 ግራም አካባቢ ነው፡፡“ከላይ የተጠቀሱት የሰቅሎች ሚዛን 15 ኪሎ ግራም ብር አካባቢ ይሆናል”(ቁጥሮች የሚለውንና መፅሐፍ ቅዱሳዊ ገንዘብ የሚለውን ይመልከቱ)

የመቤዣ ገንዘብ

ይሄ የሚያመለክተው ሙሴ የሰበሰበውን ገንዘብ ነው፡፡

ለእርሱ ልጆች

እዚህ ላይ “የእርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አሮንን ነው፡፡

በእግዚአብሔርን ቃል መሠረት ተግባራዊ እንዲያደርግ ተነገረው፤እግዚአብሔር እንዳዘዘው

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ተቀናጅተው የተነገሩትም ለጉዳዩ አፅንኦት ለመስጠት ሲባል ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔርን ቃል መሠረት ተግባራዊ እንዲያደርግ ተነገረው

እዚህ ላይ “የእግዚአብሔር ቃል” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ለሙሴ የተናገረውን እግዚአብሔርን ነው፡፡(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 4

1 ያህዌ ለሙሴና ለአሮን እንዲህ አላቸው፡፡ 2 “ከሌዋውያን መሃል የቀዓት ትውልዶችን ወንዶችን፣ በነገድ እና በየአባቶቸው ቤተሰቦች ቁጠሩ፡፡ 3 ከሰላሳ እስከ አምሳ አመት ዕድሜ ያላቸውን ወንዶች ሁሉ ቁጠሩ፡፡ እነዚህ ወንዶች በመገናኛው ድንኳን ሥራ ያገለግሉ ዘንድ ይምጡ፡፡ 4 የቀዓት ትውልድ በመገናኛው ድንኳን ለእኔ የተለዩትን እጅግ ቅዱስ የሆኑ ነገሮች ይጠብቁ፡፡ 5 ህዝቡ ጉዞውን ለመቀጠል ሲነሳ፣ አሮንና ልጆቹ ወደ ድንኳን ውስጥ ይግቡ፣ ቅድስቱን ከቅድስተ ቅዱሳን የሚለየውን መጋረጃ ያውርዱት፣ ከዚያም የቃልኪዳኑን ታቦት ምስክር በእርሱ ይሸፍኑት፡፡ 6 ታቦቱን በአስቆጣ ቁርበት ይሸፍኑት፡፡ በሰማያዊ ጨርቅ ይሸፍኑት፡፡ ለመሸከም ምሰሶ ያስገቡበት፡፡ 7 በህብስት ማቅረቢያው ጠረጴዛ ላይ ሰማያዊ ጨርቅ ያንጥፉበት፡፡ በላዩ ድስቶቹን፣ ማንኪያዎችን እና ለመቅጃ ገንቦ ያስቀምጡበት፡፡ 8 በጠረጴዛው ላይ ህብስት አይታጣ፡፤ በደማቅ ቀይ ጨርቅ እና እንደገና በአቆስጣ ቁርበት ይሸፍኗቸው፡፡ ጠረጴዛውን ለመሸከም ምሰሰዎች ያስገቡ፡፤ 9 ሰማያዊ ጨርቅ ወስደው የመቅረዝ መያዣውን ይሸፍኑ፣ ከመብራቶቹ ጋር፣ መቆንጠጫ፣ ዝርግ ሰሃኖች፣ እና ለመብራቶቹ የዘይት ገንቦዎችን ይውሰዱ፡፡ 10 መቅረዞቹንና መገልገያዎቹን በአቆስጣ ቁርበት መሸፈኛ ውስጥ ያድርጉ፣ ከዚያም በመሸከሚያ መያዣ ላይ ያስቀምጡቱ፡፡ 11 በወርቅ መሰዊያው ላይ ሰማያዊ ጨርቅ ያንጥፉ፡፤ እርሱንም በአቆስጣ ቁርበት ይሸፍኑት፣ ከዚያ መሸከሚያ ምሰሶ ያስገቡበት፡፡ 12 ዕቃዎቹን ሁሉ ለሥራ ወደተቀደሰው ስፍራ ይውሰዱና በሰማያዊ ጨርቅ ይጠቅልሉ፡፡ በአስቆጣ ቁርበት ሸፍነው ዕቃዎቹን በመሸከሚያ መያዣ ላይ ያስቀምጡ፡፡ 13 ከመሰዊያው አመዱን ያራግፉና ሐምራዊ ጨርቅ በመሰዊያው ላይ ያንጥፉ፡፡ 14 በመሰዊያው ላይ የሚጠቀሙባቸውን መሳሪያዎች ሁሉ በመሸከሚያው መሎጊያ ላይ ያስቀምጡ፡፡ እነዚህ ዕቃዎች፣ የእሳት ማንደጃዎች፣ ሜንጦዎች የእሳት መጫሪያዎች፣ ጎድጓዳ ሳህኖች፣ እና ለመሰዊያው የሚያገለግሉ ሌሎች መሳሪያዎች ናቸው፡፡ መሰዊያውን የአስቆጣ ቁርበት ይሸፍኑትና ከዚያ መሸከሚያ ምሰሶ ያስገቡበት፡፡ 15 አሮንና ልጆቹ ቅዱሱን ስፍራና መገልገያዎቹን ሙሉ ለሙሉ ሸፍው ሲጨርሱ፣ እና ህዝቡ ወደፊት ሲንቀሳቀስ በዚያን ጊዜ የቀዓት ትውልዶች ቅዱሱን ስፍራ ለመሸከም ይቅረቡ፡፡ የተቀደሱ ዕቃዎችን ከነኩ ይገደሉ፡፡ የቀዓት ትውልዶች የሥራ ድርሻ በመገናኛው ድንኳን የሚገኙ መገልገያዎችን መሸከም ነው፡፡ 16 የካህኑ የአሮን ልጅ አልዓዛር ለመብራት የሚሆነውን ዘይት ያዘጋጃል፡፡ የጣፋጩን እጣን ዝግጅት ይቆጣጠራል፣ መደበኛውን የእህል ቁርባን፣ የቅባት ዘይቱን፣ ጠቅላላውን ቤተ መቅደስ እና በውስቱ ያሉትን ሁሉ፣ እንዲሁም በቅዱስ መገልገያዎችና ቁሳቁሶች ላይ ሀላፊነት ይኖረዋል፡፡” 17 ያህዌ ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፣ 18 “የቀዓት የጎሳ ነገዶች ከሌዋዊያን መሃል እንዲወገዱ አትፍቀዱ፡፡ 19 በህይወት ይኖሩ ዘንድ እንጂ እንዳይሞቱ ይህን በማድረግ ጠብቋቸው፡፡ እጅግ ወደ ተቀደሱ ነገሮች ሲቀርቡ 20ለአፍታ እንኳን የተቀደሰውን ስፍራ ለማየት ወደ ውስጥ አይግቡ፣ አሊያ ይሞታሉ፡፡ 20 አሮንና ልጆቹ ወደ ውስጥ ይግቡ፣ ከዚያ አሮንና ልጆቹ ለእያንዳንዱ ቀዓታዊ የሚሰራውን ሥራ ይስጡት፣ ለእያንዳንዳቸው የየራሳቸውን ተግባራት ይስጧቸው፡፡ 21 ያህዌ እንደገና ሙሴን እንዲህ አለው፣ 22 “ጌድሶናውያንንም በአባቶቻቸው ቤተሰቦች፣ በየነገዳቸው ቁጠራቸው፡፡ 23 ከሰላሳ እስከ አምሳ አመት ዕድሜ ያላቸውን ቁጠራቸው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ማገልገል የሚችሉትን ሁሉ ቁጠራቸው፡፡ 24 የጌድሶናውያን ነገዶች ሲያገለግሉና ሲሸከሙ ተግባራቸው ይህ ነው፡፡ 25 የመቅደሱን መጋረጃዎች ይሸከሙ፣ የመገናኛውን ድንኳን፣ መሸፈኛውን፣ በላዩ ላይ የሚገኘውን የአቆስጣ ቁርበት መሸፈኛ እና ለመገናኛው ድንኳን መግቢያ የሚሆኑትን መገረጃዎች ይሸከሙ፡፡ 26 የአደባባዩን መጋረጃ ይሸከሙ የአደባባዩን መግቢያ መጋረጃ፣ በቤተ መቅደሱና በመሰዊያው አጠገብ ያሉትን፣ ገመዶቻቸውን፣ ለአገልግሎታቸው የሚጠቀሙባቸውን መሳሪያዎች ሁሉ ይሸከሙ፡፡ በእነዚህ ነገሮች መደረግ ያለበትን ሁሉ፣ እነርሱ ያድርግ፡፡ 27 አሮንና ልጆቹ የጌድሶናውያን ትውልዶች ማገልገል ያለባቸውን አገልግሎት ይምሯቸው፡፡ በሚያጓጉዟቸው ነገሮች ሁሉ፣ በሁሉም አገልግሎቶቻቸው ይምሯቸው፡፡ ያለባቸውን ሀላፊነቶች ሁሉ ትሰጧቸዋላችሁ፡፡ 28 ለመገናኛው ድንኳን የጌድሶናዊያን ነገድ ትውልዶች አገልግሎት ይህ ነው፡፡ የካህኑ የአሮን ልጅ ኢታምር በአገልግሎታቸው ይምራቸው፡፡ 29 የሜራሪ ትውልዶችን በነገዳቸው ቁጠራቸው፣ በአባቶቻቸው ቤተሰቦችም እዘዛቸው፣ 30 ከሰላሳ አመት እስከ አምሳ አመት ዕድሜ ያላቸውን ቁጠራቸው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ለማገልገል የሚመጡትን ሁሉ ቁጠር፡፡ 31 በመገናኛው ድንኳን የሚሰጧቸው አገልግሎቶችና የሥራ ድርሻቸው ይህ ነው፡፡ ቤተ መቅደሱን ለማስጌጥ እንክብካቤ ያድርጉ፣ የድንኳኑን ወርዶችና ቋሚዎች እና ካስማዎች ይሸከማሉ፣ 32 በቤተ መቅደሱ ዙሪያ ከሚገኙ ቋሚዎች ጋር፣ ችካሎቻቸውን፣ ካስማዎችን እና ገመዶቻቸውን ከተለያዩ መገልገያዎች ጋር ይሸከማሉ፡፡ መሸከም ያለባቸውን ቁሶች በስም ዘርዝር፡፡ 33 የሜራሪ ነገድ ትውልዶች በካህኑ በአሮን ልጅ በኢታምር መሪነት በመገናኛው ድንኳን የሚሰጡት አገልግሎት ይህ ነው፡፡” 34 የማህበሩ መሪ የሆኑት ሙሴና አሮን የቀዓታውያንን ትውልዶች በአባቶቻቸው ቤተሰቦች ነገዶች ቁጠሯቸው፡፡ 35 ሰላሳ አመት ዕድሜ የሞላቸውንና ከዚያ በላይ እስከ አምሳ አመት ዕድሜ ያላቸውን ቁጠሯቸው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ለማገልገል የሚመጡትን ሁሉ ቁጠሯቸው፡፡ 36 በየነገዳቸው 2750 ወንዶች ቁጠሩ፡፡ 37 ሙሴና አሮን በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ቀዓታዊያንን ወንዶች ሁሉ በየነገዳቸውና በየቤተሰባቸው ቁጠሩ፡፡ ይህን በማድረግ ያህዌ በሙሴ በኩል እንዲሰሩት ያዘዛቸውን አደረጉ፡፡ 38 የጌድሶናውያን ትውልዶች በየነገዳቸው፣ በየአባቶቻቸው ቤተሰቦች ተቆጠሩ፣ 39 ዕድሜያቸው ከሰላሳ እስከ አምሳ አመት የሆኑ በመገናኛው ድንኳን ለማገልገል የመጡ እያንዳንዳቸው ተቆጠሩ፡፡ 40 በየነገዳቸው እና በየአባቶቻቸው ቤተሰቦች የተቆጠሩት ወንዶች ቁጥር 2630 ነበሩ፡፡ 41 ሙሴና አሮን በመገናኛው ድኗን የሚያገለግሉትን የጌድሶናውያንን ነገዶች ትውልዶች ቆጠሩ፡፡ ይህን በማድረግ፣ ያህዌ በሙሴ በኩል እንዲሰሩት ያዘዛቸውን አደረጉ፡፡ 42 የሜራሪያውያን ትውልዶች፣ በየነገዳቸውና በየአባቶቻቸው ቤተሰቦች ተቆጠሩ፣ 43 ዕድሜያቸው ከሰላሳ እስከ አምሳ የሆኑ በመገናኛው ድንኳን ለማገልገል የመጡ እያንዳንዳቸው ተቆጠሩ፡፡ 44 በየነገዳቸው እና በየአባቶቻቸው ቤተሰቦች የተቆጠሩት ወንዶች ቁጥር 3200 ነበሩ፡፡ 45 ሙሴና አሮን በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉትን የሜራሪ ትወልዶች የሆኑትን እነዚህን ወንዶች ሁሉ ቆጠሩ፡፡ ይህን በማድረግ፣ ያህዌ በሙሴ በኩል እንዲሰሩት ያዘዛቸውን አደረጉ፡፡ 46 ስለዚህም ሙሴ፣ አሮን፣ እና የእስራኤል መሪዎች ሁሉንም ሌዋውያን በየነገዳቸው በየአባቶቻቸው ቤተሰቦች ቆጠሯቸው 47 ከሰላሳ እስከ አምሳ አመት ዕድሜ ያላቸውን ቆጠሯቸው በቤተ መቅደስ ውስጥ ማገልገል የሚችሉትን፣ እና በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የሚገኙ ዕቃዎችን መንከባከብና መሸከም የሚችሉትን እያንዳንዳቸውን ቆጠሯቸው፡፡ 48 በጠቅላላው 8580 ወንዶች ቆጠሩ፡፡ 49 በያህዌ ትዕዛዝ፣ ሙሴ እያንዳንዱን ወንድ ቆጠረ፣ እያንዳንዱን በተሰጠው የሥራ አይነት መሰረት ቆጠረ፡፡ እያንዳዱን ሰው በሚሸከመው ሀላፊነት አይነት ቆጠረ፡፡ ይህን በማድረግ ያህዌ በሙሴ በኩል ያዘዛቸውን በመስራት ያህዌ ያዘዘውን አደረጉ፡፡



Numbers 4:1

ቀአት

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ከሠላሣ ዓመት ጀምሮ እስከ ሃምሣ ዓመት ድረስ

“ከ30 እስከ 50 ዓመት ድረስ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ጉባዔውን ይቀላቀሉ

“ጉባዔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በመገናኛው ድንኳን ውስጥ እየሰሩ ያሉትን ሰዎች ነው፡፡

የእኔ የሆነውን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በተለየ ሁኔታ ለእኔ የመረጥኩትን”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:5

ሠፈሩ ዝግጅት በሚያደርግበት ወቅት

እዚህ ላይ “ሠፈር”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በሠፈሩ ውስጥ የሚገኙትን ሰዎች ነው፡፡“ሰዎቹ ዝግጅት በሚያደርጉበት ወቅት” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ከሠፈሩ በተነሱ ጊዜ

ይሄ የሚያመለክተው ሰዎች ወደ ሌላ ሥፍራ መጓዛቸውን ነው፡፡“ወደ ሌላ ሥፍራ መጓዝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የምሥክሩንም ታቦት በእርሱ ይጠቅሉለበት

“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ቅድስተ ቅዱሳኑን ከቅዱስ ቦታ የሚለየውን ነው፡፡

መሎጊያዎችን ያግቡ

የመገናኛ ድንኳኑን እንዲሸከሙ ለማስቻል መሎጊያዎቹ ከመገናኛው ድንኳኑ ጎን በቀለበት ውስጥ እንዲገቡ ይደረጋል፡፡ይሄ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“መሎጊያዎቹን ከመገናኛ ድንኳኑ ጎን በሚገኙት ቀለበት ውስጥ አስገባቸው” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:7

የገፅ ሕብስት

ሕብስቱ የእግዚአብሔርን ሕልውና የሚወክል ነው፡፡“የእግዚአብሔር የመገኘት ሕብስት” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእርሱ ላይ ይዘርጉበት

“በእርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሰማያዊውን መጎናፀፊያ ነው፡፡

ለማፍሰስ ጭልፋዎቹንና መቅጃዎቹን

የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ፍቺ የበለጠ ግልፅ ሊሆን ይችላል፡፡“ወጪቶችና” እና“ፅዋዎች”የመጠጥ ቁርባንን ለማቅረብ አገልግሎት ይሰጡ ነበር፡፡” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱን ሊሸፍኗቸው ይገባል

እነርሱን የሚለው ቃል ወጭቶቹን፤ጭልፋዎቹን፤ፅዋዎቹንና መቅጃዎቹን የሚያመለክት ነው፡፡

ሁልጊዜም የሚኖር እንጀራ በእርሱ ላይ ይሁን

እንጀራ ዘወትር ሊኖር ይገባል፡፡

ቀይ መጎናፀፊያ

“ቀይ ልብስ”

መሎጊያዎቹን ያግቡ

ጠረጴዛውን መሸከም ይችሉ ዘንድ መሎጊያዎቹ በጠረጴዛው ጠርዞች ላይ በቀለበት ውስጥ እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡ይሄ የበለጠ እንዲብራራ ማድረግ ይቻላል፡፡“መሎጊያዎቹን በጠረጴዛው ጠርዞች ላይ በቀለበት ውስጥ አስገቡት” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:9

በአስቆጣ ቁርበት መሸፈኛ ውስጥ ያድርጉት

“በአስቆጣ ቁርበት..መሸፈን ይኖርባቸዋል”

በመሸከሚያም ላይ ያድርጉት

“መሸከም ይችሉ ዘንድ እነዚህን ነገሮች ሁሉ በመሸከሚያ ላይ ማድረግ ይኖርባቸዋል”

የመሸከሚያ መሎጊያዎቹን ያግቡ

ጠረጴዛውን መሸከም ይችሉ ዘንድ መሎጊያዎቹ በመሠዊያው አጠገብ ባለው ሥፍራ ላይ በቀለበት ውስጥ እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡“የመሸከሚያ መሎጊያዎቹን በመሠዊያው ጎን ባሉት ቀለበቶች ላይ አስገቧቸው፡፡” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:12

መሸከሚያ

ዕቃዎችን ለመሸከም እንዲቻል ከመሎጊያዎች የተሰራ አራት ማዕዘን እንጨት፡፡

በመቅደስ ውስጥ ሥራ የሚያገለግሉበትን

“ሥራ”የሚለው ቃል አሕፅሮተ ሥም ሲሆን “ማገልገል” በሚለው ሥም ሊገለፅ የሚችል ነው፡፡“እግዚአብሔርን በመቅደስ ውስጥ በሚያገለግሉበት ወቅት ጥቅም ላይ የሚውል” (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ለመሠዊያው ሥራ

“ሥራ”የሚለው ቃል (አሕፅሮተ ሥም ሲሆን “ማገልገል” በሚለው ሥም(ሰዋሰው) ሊገለፅ የሚችል ነው፡፡“ “በመሠዊያው ላይ አገልግሎት በሚካሄድበት ወቅት” (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ))

የመሸከሚያ መሎጊያዎቹን ያስገቡ

መሠዊያውን መሸከም ይችሉ ዘንድ መሎጊያዎቹ በመሠዊያው አጠገብ በሚገኙት ቀለበቶች ውስጥ እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡ይሄንን የበለጠ ማብራራት ይቻላል፡፡“የመሸከሚያ መሎጊያዎቹን በመሠዊያዎቹ ጎን ባሉት ቀለበቶች ውስጥ አስገቧቸው” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:15

ቤተመቅደሱን መሸከም

እዚህ ላይ ቤተመቅደሱ የሚያመለክተው አሮንና ልጆቹ በልብሶችና በቆዳዎች የሸፈኗቸውን ዕቃዎች ሁሉ ነው፡፡“የቤተመቅደሱን ዕቃዎች ሁሉ መሸከም” (ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

ከሠፈሩም ሲነሱ

እዚህ ላይ ሠፈር የሚለው ቃል የሚያመለክተው በሠፈሩ ውስጥ ያሉትን ሰዎች ሁሉ ነው፡፡“ሰዎች ወደፊት በሚጓዙበት ወቅት” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ቀአት

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የመቅደሱን ዕቃዎች

“የተቀደሰውን ዕቃ”

ለብርሃኑ ዘይት

እዚህ ላይ “ብርሃን”የሚለው ቃል የሚያመለከተው “መብራትን”ነው፡፡“ለመብራቶቹ የሚያስፈልግ ዘይት” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

መጠበቅ

“መጠበቅ” የሚለው አሕፅሮተ ሥም እንደ ሥም(ሰዋሰው) ሊገለፅ ይችላል፡፡“የሚጠብቁት ሰዎች” (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:17

የቀአት ወገኖች

ይሄ የሚያመለክተው የቀአትን የዘር ሐረግ ነው፡፡በኦሪት ዘኁልቁ 3፡27 ላይ ይሄንን እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ከሌዋውያን መካከል መጥፋት

ይሄ ሐረግ የሚያመለክተው የቀአታውያንን ሞት ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ “ከሌዋውያን ወገን ፈፅሜ እንዳጠፋቸው ምክኒያት የሚሆኑትን ነገሮች የሚያደርጉትን ሁሉ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህንን በማድረግ

ይሄ ሐረግ የሚያመለክተው እግዚአብሔር ቀጥሎ ስለሚናገረው ነገር ነው፡፡ሙሴ ቀአታውያን እንዳይጎዱ ለመከላከል ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ እንዳይገቡ ያግዳቸዋል፡፡

ለሥራውና ለተለየ ተግባሩ

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ተቀናጅተው የቀረቡትም ለጉዳዩ አፅንኦት ለመስጠት ሲባል ነው፡፡

Numbers 4:21

የጌድሶን ትውልዶች

ይሄ የሚያመለክተው ወንዶችን ብቻ ነው፡፡“የጌድሶን የወንድ ትውልዶች” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ጌድሶን

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ከሠላሳ ዓመት ጀምሮ እስከ ሃምሳ ዓመት ድረስ

“ከ30 ዓመት እስከ 50 ዓመት”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የመገናኛውን ድንኳን ሥራ ይሰሩ ዘንድ የተሰባሰቡትን ሰዎች የሚቀላቀሉትን

“የተሰባሰቡት“የሚለው ቃል የሚያመለክተው በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ ለሥራ የቀሩትን ሰዎች ነው፡፡ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 4፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 4:24

ይሄ የነገዶች ሥራ ነው….በሚያገለግሉበትና በሚሸከሙት ነገር

ይሄ ዓረፍተ ነገር የሚቀጥሉት ቁጥሮች ስለ ምን እንደሚናገሩ መግለጫ የሚሰጥ ነው፡፡

ጌድሶናውያን

ይሄ የሚያመለክተው የጌድሶናውያንን ትውልድ ነው፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 3፡21 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በላዩም ያለውን የአስቆጣውን ቁርበት

ይሄ በመገናኛው ድንኳኑ ላይ የሚደረግ የውጪ ሽፋን ነው፡፡“በዚያ ላይ የሚደረግ የአስቆጣ ቁርበት”ወይም “በአስቆጣ ቁርበት የሚሰራ የላይኛው መሸፈኛ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእነዚህ ነገሮች የሚደረጉ ነገሮች ሁሉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለእነዚህ ሥራዎች የሚያስፈልጉ ነገሮች ሁሉ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:27

የጌድሶናውያንን ትውልዶች አገልግሎት ሁሉ መምራት ይገባል

“የጌድሶናውያን ትውልዶችን በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ እግዚአብሔርን እንዴት ማገልገል እንዳለባቸው ልትነግሯቸው ይገባል፡፡

የጌድሶናውያን ትውልዶች በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ያላቸው አገልግሎት ይሄ ነው

እዚህ ላይ “አገልግሎት”በሥም ሊገለፅ የሚችል አሕፅሮተ ሥም ነው፡፡“ይሄ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔር አሁንም እየተናገረ ስላለው ነገር ነው፡፡“የጌድሶናውያን ትውልዶች በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ የሚያገለግሉት እንደዚህ ነው”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ኢታምር

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 4:29

የሜራሪ ትውልዶች

ይሄ የሚያመለክተው ወንዶችን ብቻ ነው፡፡“የሜራሪ የወንድ ትውልዶች” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ሜራሪ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ቁጠራቸው

“ስማቸውን ዘርዝር”

ከሠላሳ ዓመት ጀምሮ እስከ ሃምሳ ዓመት ድረስ

“የ30 ዓመት ዕድሜ…የ50 ዓመት ዕድሜ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የመገናኛውን ድንኳን ሥራ ይሰሩ ዘንድ የተሰባሰቡትን ሰዎች የሚቀላቀሉትን

“የተሰባሰቡት“የሚለው ቃል የሚያመለክተው በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ ለሥራ የቀሩትን ሰዎች ነው፡፡ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 4፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 4:31

ይሄ የእነርሱ ኃላፊነት ነው

“ይሄ ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔር ቀጥሎ ሊናገር ስላለው ነገር ነው፡፡

ሳንቃዎቹ፤መወርወሪያዎቹ፤ተራዳዎቹ እነርሱን ከሚሰሩት ጠንካራ ማያዣዎች ጋር

እዚህ ላይ “እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የአዳራሹን ምሰሶዎች ነው፡፡

አውታሮቹ፤ካስማዎቹ፤ሳንቃዎቹ…እና ገመዶቻቸው

እነዚህ ሁሉ የመገናኛ ድንኳኑ ክፈፎች ናቸው፡፡እነዚህን ክፍሎች ሁሉ እንዴት እንደተረጎማችኋቸው ተመልከቱ፡፡(ኦሪት ዘኁልቁ 4፡31-32 ይመልከቱ)

የሸክማቸውን ዕቃ ሁሉ በስማቸው ቁጠሩ

“መሸከም የሚገባውን ዕቃ በእያንዳንዱ ወንድ ስም መዝግቡት”

Numbers 4:33

ከካህኑ ከአሮን ልጅ ከኢታምር እጅ በታች

“እጅ በታች”የሚለው ቃል በሥም(ሰዋሰው) የሚገለፅ አሕፅሮተ ሥም ነው፡፡“በካህኑ በአሮን ልጅ በኢታምር ትዕዛዝ መሠረት” (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ኢታምር

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 4:34

የቀአት ትውልዶች

ይሄ የሚያመለክተው ወንዶቹን ብቻ ነው፡፡“የቀአት የወንድ ትውልዶች”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ቀአታውያን

ይሄ የሚያመለክተው የቀአትን ትውልዶች ነው፡፡ይሄንን በኦሪት ዘኁልቁ 43፡27 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ሠላሳ ዓመት…ሃምሳ ዓመት

“30 ዓመት…50 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ አገልግሎት የሚገቡ ሰዎች ሁሉ

እዚህ ላይ “የሚገቡ”የሚለው ቃል ወንዶቹ “በራሳቸው ምርጫ” ያደረጉት ነገር ነው ማለቱ ሣይሆን እዚያ ስብስብ ውስጥ እንዲገቡ “መመደባቸውን”ነው የሚያሣየው፡፡“ማህበሩን እንዲቀላቀሉ የተመደቡት ሰዎች ሁሉ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አገልግሎት ለመስጠት ማህበሩን መቀላቀል

“ማህበር”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ ለመሥራት የቀሩትን ሰዎች ነው፡፡ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 4፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

2,750 ወንዶች

“ሁለት ሺህ ሰባት መቶ ሃምሳ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:38

የጌድሶን ትውልዶች

ይሄ የሚያመለክተው ወንዶቹን ነው፡፡“የጌድሶን የወንድ ትውልዶች” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የጌድሶን ትውልዶች ተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡“የጌድሶንን ትውልድ የቆጠሩት ሙሴና አሮን ናቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሠላሳ ዓመት ጀምሮ እስከ ሃምሳ ዓመት ድረስ

“ከ30 እስከ 50 ዓመት ድረስ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ አገልግሎት የሚገቡ ሰዎች ሁሉ

እዚህ ላይ “የሚገቡ”የሚለው ቃል ወንዶቹ “በራሳቸው ምርጫ” ያደረጉት ነገር ነው ማለቱ ሣይሆን እዚያ ስብስብ ውስጥ እንዲገቡ “መመደባቸውን”ነው የሚያሣየው፡፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አገልግሎት ለመስጠት ማህበሩን መቀላቀል

“ማህበሩን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ ለመሥራት የቀሩትን ሰዎች ነው፡፡ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 4፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በየነገዳቸው አንፃር ተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴና አሮን በየወገናቸው የቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

2,630

“ሁለት ሺህ ስድስት መቶ ሠላሳ”ይሄ የሚያመለክተው 2,630 ሰዎች መሆናቸውን ነው፡፡(ቁጥሮች የሚለውንና ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:41

እነርሱ ታዘዙ

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴንና አሮንን ነው፡፡

Numbers 4:42

የሜራሪ ትውልዶች ተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴና አሮን የሜራሪን ትውልዶች ቆጠሩ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሠላሳ ዓመት ጀምሮ እስከ ሃምሳ ዓመት ድረስ

“ከ30 ዓመት ጀምሮ እስከ 50 ዓመት ድረስ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ አገልግሎት የሚገቡ ሰዎች ሁሉ

እዚህ ላይ “የሚገቡ”የሚለው ቃል ወንዶቹ “በራሳቸው ምርጫ” ያደረጉት ነገር ነው ማለቱ ሣይሆን እዚያ ስብስብ ውስጥ እንዲገቡ “መመደባቸውን”ነው የሚያሣየው፡፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አገልግሎት ለመስጠት ማህበሩን መቀላቀል

“ስብስብ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ ለመሥራት የቀሩትን ሰዎች ነው፡፡ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 4፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡

በየነገዳቸውተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴና አሮን ከየነገዳቸው አንፃር የቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

3,200 ተቆጠሩ

“ሶስት ሺህ ሁለት መቶ ተቆጠሩ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:45

እነርሱ ታዘዙ

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴንና አሮንን ነው፡፡

Numbers 4:46

ከሠላሳ ዓመት ጀምሮ እስከ ሃምሣ ዓመት ድረስ

ይሄ የሚመለክተው ወንዶቹን ነው፡፡“ከሠላሳ እስከ ሃምሣ ዓመት ዕድሜ ላይ ያሉ ወንዶች”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

8,580 ወንዶች

“ስምንት ሺህ አምስት መቶ ሰማንያ ወንዶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 4:49

በእግዚአብሔር ትዕዛዝ

“እግዚአብሔር እንዳዘዘው”

እንደማንነታቸው እያንዳንዳቸውን መቁጠር….እያንዳንዱን ወንድ ከሚሸከመው ኃላፊነት አንፃር ቆጠራቸው

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ ዓይነት ትርጉም ያላቸው ሲሆን ሙሴ ወንዶቹን እንዴት እንደቆጠራቸው አፅንኦት ለመስጠት ሲባል የተደረገ ነው፡፡

ከተመደበበት ሥራ አንፃር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ከተመደበበት የሥራ ዓይነት አንፃር”ወይም “እያንዳንዱን ሰው ከመደበበት ሥራ አንፃር”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

መሸከም ይኖርበታል

“ያደርጋል”

እነርሱ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ትዕዛዝ ፈፀሙ

እዚህ ላይ “እነርሱ” እና “የሰጣቸው”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴንና አሮንን ነው፡፡


Chapter 5

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 2 “የእስራኤል ሰዎች ተላላፊ የቆዳ በሽታ ያለበትን ሁሉ፣ በስቃይ የሚመግለውን ሁሉ፣ እና ማንኛውንም በድን በመንካት ረከሰውን ሁሉ ከሰፈር እንዲያስወጡ እዘዛቸው፡፡ 3 ወንዶችም ይሁኑ ሴቶች እነዚህን ከሰፈር አስወጣቸው፡፡ እኔ በውስጡ እኖራለሁና ሰፈሩን አያርክሱ፡፡” 4 የእስራኤለ ሰዎችም ይህንኑ አደረጉ፡፡ ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው፣ ከሰፈር አስወጧቸው፡፡ የእስራኤል ሰዎች ያህዌን ታዘዙ፡፡ 5 ያህዌ ሙሴን እንደገና እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 6 “ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፡፡ አንድ ወንድ ወይም አንዲት ሴት አንዱ በሌላው ላይ በደል ሲፈጽም፣ እና ለእኔ ታማኝ ሳይሆን ሲቀር ያ ሰው በደለኛ ነው፡፡ 7 በዚህን ጊዜ በዳዩ ኃጢአቱን ይናዘዝ፡፡ በዳዩ የበደሉን ዋጋ ሙሉ ለሙሉ ይክፈል፣ ደግሞም አንድ አምስተኛውን ጨምሮ ይክፈል፡፡ ይህንን ለበደለው ይስጥ፡፡ 8 ነገር ግን ተበዳዩ ክፍያውን ለመቀበል የቅርብ ዘመድ ባይኖረው፣ በዳዩ የበደሉን ዋጋ ከአውራ በግ ጋር ለራሱ ማስተስረያ በካህኑ በኩል ለእኔ ይክፈል፡፡ 9 ከተቀደሱ ነገሮች ሁሉ የሚቀርቡ መስዋዕቶች ሁሉ፣ በእስራኤል ሰዎች ለእኔ የሚለዩ ነገሮች፣ የዚያ ካህን ይሆናሉ፡፡ 10 የእያንዳንዱ ሰው የተቀደሱ ነገሮች የካህኑ ይሆናሉ፡፡ አንድ ሰው ለካህኑ የሚሰጣቸው ማናቸውም ነገሮች የዚያ ካህን ይሆናሉ፡፡” 11 ያህዌ እንደገና ሙሴን ተናገረው፡፡ እንዲህም አለው፣ 12 “ለእስራኤል ሰዎች ተናገራቸው፡፡ እንዲህ በላቸው፣ “ምናልባት የአንድ ሰው ሚስት ወደ ሌላ ሰው ሄዳ በባሏ ላይ ኃጢአት ሰርታ ይሆናል፡፡ 13 ከባሏ ሌላ ሰው ከእርሷ ጋር ተኝቶ ይሆናል፡፡ በዚያ ሁኔታ፣ እርሷ ረክሳለች፡፡ ምንም እንኳን ባሏ ነገሩን ባያይም ወይም ስለነገሩ ባያውቅም፣ ደግሞም ድርጊቱን ስትፈጽም ማንም ባይዛትም፣ በእርሷ ላይ የሚያረጋግጥ ማንም ባይኖርም፣ 14 የሆነ ሆኖ፣ የቅናት መንፈስ ሚስቱ እንደ ረከሰች ለባልየው ይነግረው ይሆናል፡፡ ሆኖም፣ ሚስቱ ሳትረክስ የቅናት መንፈስ በሀሰት በሰውየው ላይ መጥቶ ይሆናል፡፡ 15 በዚህ ሁኔታ፣ ሰውየው ሚስቱን ወደ ካህኑ ያምጣት፡፡ ባልየው የመጠጥ ቁርባን ለእርሷ ያምጣ፡፡ የኢፍ አንድ አስረኛ የገብስ ዱቄት ያምጣ፡፡ ስለ ቅናት የሚቀርብ የእህል ቁርባን ነውና፣ምንም ዘይት ወይም እጣን አይጨምርበት፤ ምናልባት ተፈጽሞ ሊሆን ለሚችል ኃጢአት ጠቋሚ የእህል ቁርባን ነው፡፡ 16 ካህኑ ያምጣትና በያህዌ ፊት ያቁማት፡፡ 17 ካህኑ አንድ ገንቦ ቅዱስ ውሃና ከማደሪያ ድንኳኑ ወለል አፈር ይውሰድ፡፡ አፈሩን ውሃው ውስጥ ይጨምረው፡፡ 18 ካህኑ ሴትየዋን በያህዌ ፊት ያቁማት የሴትየዋን ጸጉርም ይግለጥ፡፡ ካህኑ የቅናት መስዋእት የሆነውን የእህል ቁርባን በእጇ ያስይዛታል፡፡ ካህኑ በሴትየዋ ላይ እርግማን ሊያስከትል የሚችለውን በውስጡ አቧራ ያለበትን መራራ ውሃ በእጆቹ ይያዝ፡፡ 19 ካህኑ ሴትየዋን ያስሞላት፤ እንደህም ይበላት፣ “ማንም ሰው ከአንቺ ጋር ተኝቶ ካልሆነ፣ እና ተሳስተሸ ካልሆነ እናም እርኩሰት ካልፈጸምሽ፣ እርግማን ከሚያጣው ከዚህ መራራ ውሃ በእርግጥ ነፃ ትሆኛለሽ፡፡ 20 ነገር ግን፣ አንቺ በባልሽ ስር ያለሽ ሴት፣ ተሳስተሸ ቢሆን፣ ረክሰሽ ቢሆን፣ እና ሌላ ወንድ ከአንቺ ጋር ተኝቶ ቢሆን፣ 21 ከዚያ፣ (ካህኑ በእርሷ ላይ ዕርግማን የሚያስከትል መሃላ ያስምላታል፣ ከዚያ በኋላ ሴትየዋን እንዲህ ማለቱን ይቀጥል) ‘ያህዌ ህን ማድረግሽን ለህዝብሽ በመርገምሽ ያሳያል፡፡ ያህዌ ጭንሽን ካሰለለና ሆድሽን ካሳበጠ ይህ ይታወቅ፡፡ 22 ዕርግማኑን የሚያጣው ይህ ውሃ ወደ ሆድሽ ይገባል፣ ሆድሽን ያሳብጣል፣ እንዲሁም ጭኖችሽን ያሰልላል፡፡” ሴትየዋ እንዲህ ብላ ትመልስ፣ “አሜን፣ በደለኛ ከሆንኩ ይህ በእኔ ላይ ይሁን፡፡” 23 ካህኑ እነዚህን ዕርግማኖች በጥቅል ብራና ላይ ይጻፍ፣ ከዚያ የተጻፉትን እርግማኖች በመራራው ውሃ አጥቦ ያስለቅቅ፡፡ 24 ካህኑ ዕርግማን የሚያመጣውን መራራ ውሃ እንድትጠጣ ያድርግ፡፡ ዕርግማኑን የሚያመጣው ውሃ ወደ ውስጧ ገብቶ መራራ ይሆናል፡፡ 25 የቅናት መስዋዕቱን የእህል ቁርባን ከሴትየዋ እጅ ይቀበል፡፡ የእህል ቁርባኑን በያህዌ ፊት ወደ መሰዊያው ያምጣው፡፡ 26 ካህኑ ከእህል ቁርባኑ እፍኝ ሙሉ ዘግኖ ይውሰድና በመሰዊያው ላይ ያቃጥለው፡፡ ከዚያ ለሴትየዋ መራራውን ውሃ እንድትጠጣው ይስጣት፡፡ 27 ውሃውን እንድትጠጣው ሲሰጣት በባሏ ላይ በደል በመፈፀም ረክሳ ከሆነ፣ ዕርግማን የሚያስከትለው ውሃ ወደ ውስጧ ይገባና መራራ ይሆናል፡፡ ሆዷ ያብጣል ጭኗ ይመነምናል፡፡ ሴትየዋ ከህዝቧ መሃል የተረገመች ትሆናለች፡፡ 28 ሴትየዋ የረከሰች ካልሆነችና ንጹህ ከሆነች፣ ነጻ ትሆናለች፡፡ ልጆችን መጸነስ ትችላለች፡፡ 29 የቅናት ህግ ይህ ነው፡፡ ከባሏ ውጭ ለሄደች እና ለረከሰች ሴት ህጉ ይህ ነው፡፡ 30 የቅናት መንፈስ ለያዘውና በሚስቱ ለቀና ሰው ህጉ ይህ ነው፡፡ ሴትየዋን በያህዌ ፊት ያምጣ፣ ካህኑም ይህ የቅናት ህግ የሚገልጸውን ሁሉ በእርሷ ላይ ያድርግ፡፡ 31 ሰውየው ሚስቱን ወደ ካህን በማቅረቡ ከበደል ነጻ ይሆናለ፡፡ ሴትየዋ በድላ ከሆነ ማናቸውንም በደል ትሸከማለች፡፡”



Numbers 5:1

ተላላፊ የቆዳ በሽታ

ይሄ የሚያመለክተው ቆዳን ለበሽታ የሚዳርገውንና ወደ ሌሎች ሰዎች በፍጥነት የሚዛመተውን የቆዳ በሽታ ነው፡፡

ለሕመም የሚዳርግ ፈሳሽ

ይሄ የሚያመለከተው ከተከፈተ ነገር ውስጥ የሚወጣን ፈሳሽ ነው፡፡

በሬሣም የረከሰውን ሁሉ

አንድ ሰው ሬሣ የሚነካ ከሆነ እንደረከሰ ነበር የሚቆጠረው፡፡የእግዚአብሔርን ዓላማ ለማስፈፀም ተቀባይነት የሌለው ሰው አካሉ ንፁህ እንዳልሆነ ተደርጎ ነው የሚገለፀው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እናንተ አውጧቸው

እዚህ ላይ “እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር በመሆኑ የእሥራኤልን ሕዝብ የሚያመለክት ነው፡፡

የእሥራኤልም ልጆች እንዲሁ አደረጉ

ይሄ ማለት የረከሱትን ሰዎች አስወጧቸው ማለት ነው፡፡የዚህ ሙሉ ሃሣቡ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“የእሥራኤል ሰዎች የረከሱትን ሰዎች ከሠፈራቸው ውጪ እንዲወጡ አደረጓቸው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 5:5

ሰዎች እርስ በእርሳቸው የሚያደርጓቸው ኃጢአቶች

“ሰዎች እርስ በእርስ የሚያደርጓቸው ማንኛውም ዓይነት ኃጢአቶች”

ለእኔ ታማኝ ያልሆነ

አንድ ሰው በሌላ ሰው ላይ ኃጢአትን ቢሰራ በእግዚአብሔር ላይ እንዳመፀ ስለሚቆጠር እግዚአብሔር ይሄንን ሰው ታማኝ እንዳልሆነ ሰው ይቆጥረዋል ማለት ነው፡፡“እኔንም በድለዋል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 5:8

ነገር ግን ይመልስት ዘንድ ሰውዬው ዘመድ ባይኖረው

አብዛኛውን ጊዜ የተበደለው ሰው ገንዘቡን የሚወስድ ቢሆንም ሰውዬው በሕይወት ከሌለ ግን የገንዘቡ ክፍያ ለቅርብ ዘመዱ እንዲተላለፍ የሚደረግ ይሆናል፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብረራ ይችላል፡፡“የተበደለው ሰው በሕይወት ከሌለና ገንዘቡን የሚቀበልለት የቅርብ ዘመድ የማይኖረው ከሆነ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀት ወይም የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የተበደለው ሰው ግን …

ይሄ በድርጊት መልኩ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ጥፋተኛ የተባለው ሰው የበደለ ከሆነ”

የበደሉን ዋጋ በካህኑ አማካይኝት ለእኔ ይስጥ

አንድ ሰው በበደለው በደል ምክኒያት ገንዘቡን ለካህኑ የሚሰጥ ከሆነ ለእግዚአብሔር እንደሰጠ ነው የሚቆጠረው፡፡

ማስተሰረያው ለእርሱ ይሁን

ማስተሰረያ የሚደረገው ለሰውዬው ኃጢአት ነው፡፡እዚህ ላይ እግዚአብሔር እያመለከተ ያለው ኃጢአቱን የፈፀመውን ሰው ነው፡፡“ለኃጢአቱ ማስተሰረያ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ከእሥራኤል ሰዎች ለካህኑ የሚቀርቡ የተለዩ ነገሮች

ይሄ በድርጊት መልኩ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእሥራኤል ሰዎች የተቀደሰውን ነገር ለይተው ወደ ካህኑ የሚያመጧቸው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰው ሁሉ የሚሰጠው የተቀደሰ ነገር ለካህኑ ይሆናል፤ማንኛውም ሰው ማንኛውንም ነገር ለካህኑ ቢሰጥ የካህኑ ይሆናል

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን አንድ ላይ ሆነው እንዲቀርቡ የተፈለገበት ምክኒያት አንድ ሰው የሚሰጠው የተቀደሰ ነገር ለተሰጠው ለዚያ ካህን እንደሆነ አፅንኦት ለመሥጠት ተፈልጎ ነው፡፡(ተመሣሣይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 5:11

የአንድ ሰው ሚስት ከእርሱ ፈቀቅ ብትል፤በእርሱም ላይ ብትበድል

ይሄ በመሠረቱ ሊሆን የሚችል ነገር ነው፡፡

Numbers 5:16

አቅርበው በእግዚአብሔር ፊት ያስቀምጧት

ካህኑ “በእግዚአብሔር ፊት” መሠዊያው አጠገብ ያመጣታል፡፡“በመሠዊያው አጠገብ በእግዚአብሔር ፊት ያስቀምጣታል” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 5:18

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ሕልውና ፊት”

በሚቀርበው የእህሉ ቁርባን

ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 5፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የራሳችሁን መንገድ ካልተከተላችሁ

“የራስን መንገድ መከተል” ምሣሌያዊ አነጋገር ሲሆን “ታማኝ አለመሆን”ማለት ነው፡፡ “ለባለቤትሽ ታማኝ ካልሆንሽ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ኃጢአትን ፈፀማችሁ

“ኃጢአትን በመፈፀም” ይሄ ሐረግ የሚያመለክተው “ዝሙትን ስለመፈፀም ነው”

ከዚህ መራራ ውኃ ነፃ ትሆናላችሁ

ከሆነ ነገር “ነፃ ትሆናላችሁ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በእርሱ አለመጎዳትን ነው፡፡“ሊጎዳችሁ የሚችል ውኃ ለጉዳት አይሰጣችሁም”(ምሣሌያዊ አነጋገርን የሚለውን ይመልከቱ)

መርገምን ሊያመጣ የሚችለው ይሄ መራራ ውኃ

እዚህ ላይ መራራው ውኃ መርገምን ሊያመጣ እንደሚችል ተደርጎ ተገልጿል፡፡ይሄ ማለት አንዲት ሴት ኃጢአተኛ ከሆነች ውኃውን በምትጠጣበት ወቅት ልጅ እንዳትወልድ ምክኒያት ይሆንባታል ማለት ነው፡፡“ይሄ መራራ ውኃ መርገም ሊሆንብህ ይችላል”(ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 5:20

በባሏ ሥር

ይሄ ሐረግ የሚያመለክተው በባሏ ሥልጣን ሥር መሆኗን ነው፡፡“በባሏ ሥልጣን ሥር” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የራሳችሁን መንገድ ካልተከተላችሁ

“የራስን መንገድ መከተል”የሚለው ሐረግ ምሣሌያዊ አነጋገር ሲሆን “ታማኝ አለመሆን”ማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ረክሳችኋል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሣችሁን አርክሳችኋል” (ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በላይዋ ላይ መርገምን ሊያወርድ የሚችል

“መርገምን ሊያወርድ”የሚለው ቃል ምሣሌያዊ አነጋገር ሲሆን በላይዋ ላይ መርገም ይመጣል የሚል ፍቺ ያለው ነው፡፡“በላይዋ ላይ መርገም እንዲመጣ ሊያደርግ የሚችል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ለእርግማን ይዳርግሻል…በሕዝብሽ መካከል

እዚህ ላይ ፀሐፊው የሚናገረው ሌሎች ሰዎች እንዲረግሟት መንስኤ የሚሆነውን እግዚአብሔር ለሴትዬዋ የሚሰጣትን መርገም በተመለከተ ልክ ሴትዬዋ ራስዋ መርገም እንደሆነች አድርጎ ነው የሚገልፀው፡፡“እግዚአብሔር የረገመሽ በመሆኑ ሌሎች ሰዎችም ይረግሙሻል፡፡እግዚአብሔርም በእውነት ስለመረገምሽ ሰዎች እንዲመለከቱ ያደርጋል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በዚህ መልኩ ለሕዝብሽ የሚታይ ይሆናል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”ይህንን ለሕዝብሽ እንደ እርግማን ያሣየዋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ይሄ በሕዝብሽ መካከል የሚደረግ ይሆናል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡1)ሴትዬዋ ልጅ ለመውለድ አትችልም 2)እርግዝናው የሚጨናገፍ በመሆኑ ሕፃኑ ልጅ በሕይወት አይኖርም፡፡

ጭንሽ ይሰለስላል

እዚህ ላይ “ጭን” የሚለው ቃል የሴትን ማሕፀን ወይም ሌላ የሰውነት አካሏን ለመጥራት የተጠቀሙበት ጨዋ የሆነ አገላለፅ ነው፡፡“ማሕፀንሽ ጥቅም የማይሰጥ ይሆናል”(ሥርዓት የሌለውን ነገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 5:23

የተፃፉትን መርገሞች በመራራም ውኃ ይደመስሰዋል

ይሄ ማለት ቀለሙን ከብራናው ላይ ያጥበዋል ማለት ነው፡፡

የተፃፉ መርገሞች

ይሄ በድርጊት መልከ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የፃፋቸው መርገሞች”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 5:24

አጠቃላይ መረጃ

ቁጥር 24 በአጠቃላይ የሚገልፀው ካህኑ ምን ማድረግ እንዳለበትና ሴትዬዋ ውኃውን በምትጠጣበት ወቅት ሊከሰት የሚችለውን ነገር አስመልክቶ ነው፡፡ቁጥር 25 እና 26 ካህኑ ይህንን ሥራ እንዴት ማከናወን እንደሚኖርበት በዝርዝር ያብራራል፡፡ካህኑ ውኃውን ለሴትዬዋ ከሰጣት በኋላ የምትጠጣው አንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡

የውክልና ቁርባን

አንድ እፍኝ እህል አጠቃላዩን የእህል ቁርባን ይወክላል፡፡ይሄ ማለት በጠቃላይ ቁርባኑ ለእግዚአብሔር ይሆናል ማለት ነው፡፡

የቅንአት የእህል ቁርባን

“የቅንአት የእህል ቁርባን”ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 5፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 5:27

ከፈፀመችው የተነሣ የረከሰች ከሆነ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ “ድርጊቱን ከመፈፀሟ የተነሣ የረከሰች ከሆነ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ኃጠአትን ሠርታለች

እዚህ ላይ “ኃጢአት”የሚያመለክተው በተለይ ዝሙት መፈፀምን ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ዝሙትን ሠርታለች” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ሆድዋም ይነፋል፤ጭንዋም ይሰለስላል

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1)ሴትዬዋ ልጅ ለመውለድ አትችልም 2)የሴትዋ ፅንስ ስለሚጨናገፍ ሕፃኑ ልጅ በሕይወት አይኖርም፡፡እዚህ ላይ “ጭን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የሴትን ማሕፀን ወይም የአካሏን ክፍል ነው፡፡(ሥርዓት የሌለውን ነገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ) ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 5፡21 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ሴቲቱም በሕዝብዋ መካከል ለመርገም ትሆናለች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሕዝቧ ይረግማታል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ያልረከሰች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አላረከሳትም”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ንፁህ ከሆነች

እዚህ ላይ “ጥፋተኛ አለመሆን” “ንፁህ መሆን” በሚል ቃል ይገለፃል፡፡ (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ንፁህ ትሆናለች

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1)“ከዚያ በኋላ የተረገመች አትሆንም”2)“ከዚያ በኋላ ከመርገም ነፃ ትሆናለች”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ልጅንም ታረግዛለች

“ታረግዛለች”

Numbers 5:29

የቅንአት ሕግ

“ቅንአትን የሚዳኝ ሕግ”

ከባልዋ ሸሽታ የምትሄድ

“መሸሽ”የሚለው ቃል ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ትርጉሙም “ታማኝ አለመሆን”ማለት ነው፡፡“ለባልዋ ታማኝ ያልሆነች”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ረክሳለች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራስዋን ታረክሳለች”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የቅንአት መንፈስ

ይሄ የሚያመለክተው የሰውን የቅንአት አስተሳሰብና ስሜቶችን ነው፡ይህንን በዘኁልቁ 5፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡“ቅንአት ያለበት ሰው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ስለ ሚስቱም በቀና ጊዜ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ሚስቱ ከሌላ ሰው ጋር በመተኛት ታማኝ አለመሆኗን መጠርጠር ማለት ነው፡፡“ሚስቱ ለእርሱ ታማኝ እንዳልሆነች ይጠረጥራል” ወይም “ከሌላ ሰው ጋር እንደተኛች ይጠረጥራል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ህልውና ፊት”

Numbers 5:31

ሚስቱን ወደ ካህኑ በማቅረቡ ከኃጢአቱ ንፁሕ ይሆናል

“ሚስቱን ወደ ካህኑ በማምጣቱ የተሳሳተ ነገር እንደፈፀመ ሰው በደለኛ አይባልም ”

መሸከም ግድ ነው

“መከራውን መቋቋም ያስፈልጋል”


Chapter 6

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “ለእስራኤል ሰዎች ተናገራቸው፡፡ እንዲህ በላቸው፣ ‘አንድ ወንድ ወይም አንዲት ሴት ናዝራዊ ሆኖ ራሱን ለያህዌ በተለየ ስዕለት ሲለይ፣ 3 ከወይንና ከሚያሰክር መጠጥ ራሱን ይለይ፡፡ ከወይን ወይም ከሚያሰክር መጠጥ የተሰራ ኮምጣጤ አይጠጣ፡፡ ማናቸውንም የወይን ጭማቂ አይጠጣ ወይም የወይን ፍሬ ወይም ዘቢብ አይብላ፡፡ 4 ለእኔ በተለየባቸው ቀናት ሁሉ፣ ከፍሬያቸው ግልፋፊ የተሰራ ማናቸውንም ነገር ጨምሮ ከወይን የተሰራ ምንም ነገር አይብላ፡፡ 5 ለያህዌ ራሱን የለየባቸው ቀናት እስኪያበቁ ድረስ በስለቱ ጊዜያት ሁሉ ራሱን ምላጭ አይንካው፡፡ ለያህዌ የተለየ ይሁን፡፡ ፀጉሩ በራሱ ላይ እንዲያድግ ይተወው፡፡ 6 ራሱን ለያህዌ በለየባቸው ጊዜያት ሁሉ፣ ወደ ሞተ ሰው አይቅረብ፡፡ 7 አባቱ፣ እናቱ፣ ወንድሙ ወይም እህቱ ቢሞቱ እንኳን ራሱን ማርከስ የለበትም፡፡ ይህም የሚሆነው ማንም ሰው በረጅም ጠጉሩ እንደሚመለከተው፣ ለእግዚአብሔር የተለየ ነው፡፡ 8 በተለየበት ጊዜ ሁሉ ለያህዌ የተለየ ቅዱስ ነው፡፡ 9 አንድ ሰው ድንገት አጠገቡ ቢሞት እና ማንነቱን የለየበትን ፀጉሩን ቢያረክስበት፣ መንጻት ባለበት ከሰባተኛው ቀን በኋላ ራሱን ይላጭ፡፡ ራሱን መላጨት ያለበት በዚያን ጊዜ ነው፡፡ 10 በስምተኛው ቀን ሁለት ርግቦች ወይም ሁለት ዋኖሶች ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ ለካህኑ ያቅርብ፡፡ 11 ካህኑ አንዱን ወፍ ለኃጢአት መስዋዕት ሌላውን የሚቃተል መስዋዕት አድርጎ ያቅርብ፡፡ ሬሳ አጠገብ በመሆን ኃጢአት ሰርቷልና እነዚህ ለእርሱ ስርየት ይቀርባሉ፡፡ በዚያው ዕለት ራሱን መልሶ ለያህዌ ይስጥ፡፡ 12 ለተለየበት ጊዜ ራሱን ለያህዌ መልሶ ይስጥ፡፡ ለበደል መስዋዕት የአንድ አመት ወንድ ጠቦት ያምጣ፡፡ ራሱን ከማርከሱ በፊት የነበሩ ቀናት አይቆጠሩም፣ ምክንያቱም ለእግዚአብሔር ተለይቶ ባለበት ጊዜ ረክሷል፡፡ 13 ናዝራዊ መለየቱ ስለሚያበቃበት ጊዜ የተሰጠው ህግ ይህ ነው፡፡ ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ ያምጡት፡፡ 14 መስዋዕቱን ለያህዌ ያቅርቡ ነውር የሌለበት የአንድ አመት ወንድ ጠቦት የሚቃጠል መስዋዕት አድርጎ ያቅርብ፡፡ ለህብረት መስዋዕት ነውር የሌለበት አውራ በግ ያምጣ፡፡ 15 እንደዚሁም እርሾ ያልገባበት አንድ መሶብ ዳቦ፣ በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት ዳቦዎች፣ በዘይት የተቀባ እርሾ የሌለበት የገብስ ቂጣ፣ ከእህል ቁርባንና ከመጠጥ መስዋዕቶች ጋር ያምጣ፡፡ 16 ካህኑ እነዚህን በያህዌ ፊት ያቅርባቸው፡፡ እርሱ የኃጢአት መስዋዕቱንና የሚቃጠል መስዋዕቱን ያቅርብ፡፡ 17 ለያህዌ የህብረት መስዋዕቱን፣ እርሾ ካልገባበት ከመሶቡ ዳቦ ጋር፣ አውራ በጉን መስዋዕት አድርጎ ያቅርብ፡፡ እንዲሁም ካህኑ የእህል ቁርባኑን እና የመጠጥ መስዋዕቱን ጭምር ያቅርብ፡፡ 18 ናዝራዊው ለእግዚአብሔር መለየቱን የሚያሳየውን ፀጉሩን በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ይላጭ፡፡ ፀጉሩን ከራሱ ወስዶ የህብረት መስዋዕቶቹ በሚቀርቡበት በሚነደው እሳት ውስጥ ይጨምረው፡፡ 19 ካህኑ የተቀቀለውን አውራ በግ ወርች፣ ከመሶቡ ውስጥ እርሾ ያልገባበትን አንድ ዳቦ፣ እና አንድ እርሾ ያልገባበት የገብስ ቂጣ ይውሰድ፡፡ ናዝራዊው መለየቱን የሚያሳየውን ጸጉሩን ከተላጨ በኋላ ካህኑ እነዚህን በእጆቹ ያስይዘው፡፡ 20 ካህኑ እነዚህን መስዋዕት አድርጎ በያህዌ ፊት ከፍ አድርጎ ያንሳቸውና ለእርሱ ያቅርባቸው፡፡ ይህ ከፍ ተደርጎ ከተነሳው ፍርምባና ከቀረበው ወርች ጋር ለካህኑ ተለየ ቅዱስ ምግብ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ናዝራዊው ወይን ሊጠጣ ይችላል፡፡ 21 ለያህዌ ለመለየት ስዕለቱን ያቀረበ ናዝራዊ ህጉ ይህ ነው፡፡ ማናቸውንም ሌሎች ነገሮች ቢሰጥ በናዝራዊነት ህግ መሠረት እንዲጠብቃቸው የተሰጡትን ቃል ኪዳኖች ለመጠበቅ የገባውን የስዕለት ግዴታዎች መጠበቅ አለበት፡፡” 22 ያህዌ እንደገና ሙሴን ተናገረው፡፡ እንዲህም አለው፣ 23 “ለአሮንና ለልጆቹ እንዲህ በላቸው፣ ‘የእስራኤልን ሰዎች በዚህ መንገድ ባርኳቸው፡፡ እንደዚህ በሏቸው፣ 24 “ያህዌ ይባርችሁ ይጠብቃችሁ፡፡ 25 ያህዌ ብርሃኑን በእናንተ ላይ ያብራራ ፊቱን ይመልስላችሁ፣ ይራራላች፡፡ 26 ያህዌ በሞገስ ያጥግባችሁ፣ ሰላምንም ይስጣችሁ፡፡’” 27 ለእስራኤል ሕዝብ ስሜን የሚያስተዋውቁት በዚህ መንገድ ነው፡፡ እኔም እባርካቸዋለሁ፡፡”



Numbers 6:1

ራሱን ይለያል…የተለየ ነው

“ራስን ለሆነ ሰው መለየት”ማለት ለዚያ ሰው “ራስን መስጠት”ማለት ነው፡፡“ይሰጣል…ራሱን ይሰጣል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ራሱን ከ…መለየት ይኖርበታል

የዚህ ፈሊጣዊ አነጋገር ትርጉም ሊጠጣቸው ወይም ሊበላቸው አይገባም ማለት ነው፡፡“መውሰድ አይገባውም”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከወይን የተገኘ ሆምጣጤ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰዎች ከወይን የሚሰሩት ሆምጣጤ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ሆምጣጤ

ይሄ ማለት ወይንና ሌላ ጠንካራ መጠጦች ለብዙ ጊዜ እንዲፈሉ ከተደረገ በኋላ መራራ የሚሆነው መጠጥ ነው፡፡

ወይም ከጠንካራ መጠጥ

ግልፅ የተደረገውን መረጃ የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡ “ወይም ሰዎች ከጠንካራ መጠጥ የሚሰሩት ሆምጣጤ”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

ዘቢብ

የደረቁ ወይኖች

ለእኔ የተለየ ነው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን ለእኔ የተለየ ያደርጋል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከወይን ያለተሰራ ነገር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰዎች ከወይን የማይሰሯቸው ነገሮች”(ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡)

ከውስጡ ፍሬ ጀምሮ እስከ ገረፎው ድረስ

እነዚህ ሁለት ፅንፍ የያዙ ነገሮች የቀረቡት በአጠቃላይ የወይን ፍሬ መበላት እንደሌለበት አፅንዖት ለመስጠት ነው፡፡“ከየትኛውም የወይን ክፍል” (ሆን ብሎ አጋኖ መናገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:5

ራስን ለመለየት ስእለት ማድረግ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“መለየት”ማለት“ራስን መስጠት”ማለት ነው፡

በራሱ ላይ ምላጭ መድረስ አይኖርበትም

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ማንም ሰው ቢሆን በራሱ ላይ ምላጭ መጠቀም የለበትም”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር የተለየበት ወራት

“መለየት” የሚለው ቃል አሕፅሮተ ሥም ሲሆን በግሥ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡እዚህ ላይ “መለየት”ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን “ለአንድ ነገር ራስን መስጠት ማለት ነው”“ራሱን ለእግዚአብሔር የለየበት ወራት”ወይም “ራሱን ለእግዚአብሔር የሰጠበት ወራት”(አሕፅሮተ ሥምንና ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር የተለየበት ወራት እስኪፈፀም ድረስ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለእግዚአብሔር የሚለይበት ወራት የመጠናቀቂያ ጊዜ አለው ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር መለየት ይኖርበታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን ለእግዚአብሔር መለየት አለበት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:6

ይለያል…ተለይቷል…መለየት

እዚህ ላይ “መለየት”ማለት“ራስን መሥጠት”ማለት ነው፡፡“ራሱን ይሰጣል..ራሱን ሰጥቷል…ራስን መሥጠት”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ንፁህ ያልሆነ

ለእግዚአብሔር ዓላማዎች ተቀባይነት የሌለው ሰው ልክ አካሉ ንፁህ እንዳልሆነ ዓይነት ተደርጎ ነው የሚገለፀው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ተለይቷል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን ለይቷል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የእርሱ መለየት

“መለየት” የሚለው አሕፅሮተ ሥም በግሥ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን የለየ በመሆኑ”

ራሱን ለእግዚአብሔር የተወ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን ለእግዚአብሔር አውሏል” ወይም “ራሱን ለእግዚአብሔር ለይቷል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:9

የተለየውንም ራሱን ቢላጭ

እዚህ ላይ “ራስ”የሚለው ቃል የሚወክለው መሐላውን በተምሣሌትነት የሚገልፀውን የናዝራዊ ሰውን ፀጉር ነው፡፡“ለእግዚአብሔር የተለየ መሆኑን ለሰዎች ሁሉ የሚያሳየውን ረዥሙን ፀጉር ይላጨዋል”ወይም “ራሱን ተላጨ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

እርሱ በሚነፃበት ቀን

“መንፃት”የሚለው አሕፅሮተ ሥም እንደ ግሥ ሐረግ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን ለእግዚአብሔር በለየበት ወቅት”(አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

በሰባተኛው ቀን

“ቀን 7”(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:10

ስምንተኛው ቀን

“ቀን 8” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:12

ራሱን የተለየ ያደረገበት ወራት

“ራሱን እንደገና ሊለይ ባለበት ቀናት”

ተባት ጠቦት…ለመሥዋዕት ማምጣት ይኖርበታል

ሰውዬው ለመሥዋዕት ይቀርብ ዘንድ ጠቦቱን ወደ ካህኑ ማምጣት ይኖርበታል፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ትርጉም የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ለበደል መሥዋዕት ይሆን ዘንድ የአንድ ዓመት ተባት ጠቦት ወደ ካህኑ ማምጣት ይኖርበታል፡፡”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ራሱን ከመላጨቱ በፊት የነበሩት ወራት የማይቆጠሩ ይሆናል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን ከመላጨቱ በፊት የነበሩት ቀናት የማይቆጠሩ ይሆናሉ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ቅድስናው ረክሷል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን አረከሰ”ወይም “ራሱን ተቀባይነት እንዳይኖረው አደረገ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:13

መለየቱ

እዚህ ላይ “መለየት”ማለት “መሰጠት”ማለት ነው፡፡ይሄ አሕፅሮተ ሥም በግሥ መልክም ሊገለፅ ይችላል፡፡ “መሠጠቱ”ወይም “ራሱን መሥጠቱ”ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

ይቅረብ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንድ ሰው ሊያቀርበው ይገባል”ወይም “መቅረብ ይኖርበታል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

መሥዋዕቱን ለእግዚአብሔር ያቅርብ

ለእግዚአብሔር መሥዋዕት ይሆን ዘንድ ቁርባኑን ወደ ካህኑ ማምጣት ይኖርበታል፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ፍቺ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“በካህኑ አማካይነት መሥዋዕት ይሆን ዘንድ መሥዋዕቱን ለካህኑ ማቅረብ ይኖርበታል፡፡”ወይም “ቁርባኑን ለእግዚአብሔር ካቀረበ በኋላ ካህኑ ይሰዋዋል፡፡”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

እርሾ የሌለበት ቂጣ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ያለ እርሾ ያዘጋጀው ቂጣ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት “

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሰው መልካም ዱቄት” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይትም የተቀባ እርሾ የሌለው ስስ ቂጣ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እርሾ የሌለው ቂጣ ሆኖ በዘይት የተለወሰ“(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እርሾ የሌለበት ቂጣ

የተቆራረጡ ጠፍጣፋ ቂጣዎች

የእነርሱን የእህል ቁርባንና የመጠጡን ቁርባን

“የእነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ናዝራዊ ሰው እንዲያመጣ የተጠየቀውን ቁርባን ነው፡፡አብዛኛውን ጊዜ የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ከሌሎች የመሥዋዕት ዓይነቶች ጋር እንዲቀርቡ ይጠየቁ ነበር፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ፍቺ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ከሌሎች የመሥዋዕት ዓይነቶች ጋር እንዲቀርቡ እግዚአብሔር የሚጠይቀው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:16

እርሱ የእርሱን የኃጢአት መሥዋዕት ያሳርጋል

“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ካህኑን ሲሆን “የእርሱ”የሚለው ቃል ደግሞ መሐላውን ያደረገውን ሰው ነው፡፡

የወዳጅነት መሥዋዕት

“እንደ ሕብረት መፍጠሪያ መሥዋዕት”

ካህኑም ደግሞ …..የመጠጥ ቁርባን ማቅረብ ይኖርበታል

ግንዛቤ የተገኘበትን መረጃ የበለጠ ልታብራራሩት ትችላላችሁ፡፡“ካህኑ የመጠጥ ቁርባኑን ….ለእግዚአብሔር ማቅረብ ይኖርበታል”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:18

መለየቱን የሚገልፀውን

እዚህ ላይ “መለየት”ማለት “መሠጠት”ማለት ነው፡፡አሕፅሮተ ሥሙ በግሥ መልክ ሊፃፍ ይችላል፡፡“መሠጠቱን የማሣወቅ”ወይም “ራሱን እንዴት እንደሰጠ ለማሣወቅ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:19

የተቀቀለውን የአውራ በግ ወርች

ይሄ እንግዲህ አውራውን በግ ቀቅሎታል ማለት ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የቀቀለው የአውራ በጉ ወርች”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

መለየትን ማሣወቅ

እዚህ ላይ “መለየት”ማለት “ራስን መሥጠት” ማለት ነው፡፡ይሄ አሕፅሮተ ሥም “ተለየ” በሚል ግሥ መገለፅ ይችላል፡፡“ራሱን መሥጠቱን ማመልከት”ወይም “ራሱን ለእግዚአብሔር መሥጠቱን ማሣወቅ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

ካህኑ እነርሱን መወዝወዝ ይኖርበታል

ዕቃዎቹን ለናዝራዊው ከሰጠው በኋላ ካህኑ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት ለማቅረብ እንደገና ከእርሱ ይቀበላቸዋል፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ከዚያ በኋላ ካህኑ እንደገና ወስዶ ሊወዘውዛቸው ይገባል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ከ..ጋር

“እርሱንም ጭምር”

ከተወዘወዘው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ካህኑ የወዘወዘው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የቀረበውን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እርሱ ያቀረበውን”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:21

የእርሱ መለየት

እዚህ ላይ “መለየት”ማለት “መሠጠት”ማለት ነው፡፡አሕፅሮት ስሙ በግሥ መልክ ሊፃፍ ይችላል፡፡“የእርሱ መሠጠት”ወይም “ራሱን ለእግዚአብሔር መለየቱ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

እጁም ከሚያገኘው ሌላ

ይሄ የሚያመለክተው አንድ ናዝራዊ የሆነ ሰው እንዲሰጥ ከታዘዘው በላይ ለመሥጠት መወሰኑን ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ተጨማሪ የሚያቀርበው ቁርባን የሚኖር ከሆነ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ስእለቱን እንደተሳለ እንዲሁ ያደርጋል

“የተሳላቸውን የስእለት መሥፈርቶች ማሟላት ይጠበቅበታል”

ሕጎቹን መጠበቅ ይኖርበታል …እንደ ናዝራዊ ሕግ መሠረት ቃሉን ለመጠበቅ

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሣሣይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን አንድ ላይ እንዲቀናጁ የተደረገው መታዘዝ እንደሚኖርበት አፅንኦት ለመስጠት ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

በናዝራዊ ሕግ በተጠቀሰው ተስፋ መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የናዝራዊ ሕግ የሚያመለክተው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:22

እናንተ የእሥራኤልን ልጆች ልትባርኳቸው ይገባል

“እናንተ”የሚለው የብዙ ቁጥር ነው፡፡(እናንተ በሚል በተለያዩ መልኮች የተገለፁትን ይመልከቱ)

ይጠብቅህ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“መጠበቅ”ማለት“መከላከል”ማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 6:25

ፊቱን ያብራልህ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ለሆነ ሰው በጎ አስተሳሰብ አለው ማለት ነው፡፡በፈገግታም ሊገለፅ ይችላል፡፡አሕፅሮት ስሙ በግሥ መልክ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ፈገግ ሲልልህ”ወይም“ወደ አንተ በቅንነት ሲመለከት”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በርህራሄ ይመልከትህ

እዚህ ላይ “ይመልከትህ”የሚለው ቃል በዚያ ሰው ላይ በጎ የሆነ አስተያያት እንዳለው የሚገልፅ ነው፡፡“አደላልህ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ፊቱን ወደ አንተ ያንሳ …ሰላምንም ይስጥህ

እዚህ ላይ “አንተ”የሚለው ቃል ነጠላ ነው፡፡(አንተ በሚል በተለያዩ መልኮች የተገለፁትን ይመልከቱ)

ስሜን መሥጠት ይኖርባቸዋል

እዚህ ላይ እግዚአብሔር “ስሜን”ሰጥቻለሁ ብሎ በመናገሩ እሥራኤላውያን የራሱ እንደሆኑ ያውጃል፡፡“የእሥራኤል ሕዝብ የእኔ መሆናቸውን ማሳወቅ ይኖርባቸዋል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 7

1 ማደሪያ ድንኳኑን በጨረሰ ቀን፣ ከመገልገያ ዕቃዎቹ ጋር ቀብቶ ለያህዌ ለየው፡፡ በመሰዊያውና በዕቃዎቹ ላይ እንዲሁ አደረገ፡፡ ቀብቶ ለያህዌ ለያቸው፡፡ 2 በዚያ ቀን፣ የእስራኤል መሪዎች፣ የአባቶቻቸው ቤተሰቦች አባቶች መስዋዕቶችን አቀረቡ፡፡ ጎሳዎቹን የሚመሩት እነዚህ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ የህዝብ ቀጠራውን ተቆጣጠሩ፡፡ 3 መስዋዕቶቻቸውን ያህዌ ፊት አመጡ፡፡ ስድስት የተሸፈኑ ሰረገሎችና አስራ ሁለት በሬዎች አመጡ፡፡ ለየሁለቱ መሪዎች አንድ ሰረገላ አመጡ፣ እያንዳንዱ መሪ አንድ በሬ አመጣ፡፡ እነርሱ እነዚህን ነገሮች በማደሪያው ድንኳን ፊት አቀረቡ፡፡ 4 ከዚያም ያህዌ ሙሴን ተናገረው፡፡ እንዲህም አለው፣ 5 “መስዋዕታቸውን ከእነርሱ ተቀበልና ለመገናኛው ድንኳን ሥራ አውላቸው፡፡ ለሥራው እንደሚያስፈልጋቸው ለእያንዳንዱ፣ መስዋዕቶቹን ለሌዋውያን ስጥ፡፡” 6 ሙሴ ሰረገሎቹንና በሬዎቹን ወስዶ ለሌዋውያኑ ሰጣቸው፡፡ 7 ለጌድሶናውያን ተውልዶች ለስራቸው እንደሚያስፈልግ ሁለት ሰረገላዎችና አራት በሬዎች ሰጠ፡፡ 8 ለሜራሪ ትውልዶች በካህኑ በአሮን ልጅ በኢታምር በኩል አራት ሰረገሎችንና ስምንት በሬዎችን ሰጠ፡፡ ይህን ያደረገው ሥራቸው ይህን ስለሚጠይቅ ነው፡፡ 9 ለቀዓት ትውዶች ከእነዚህ ነገሮች ምንም አልሰጠም፣ ምክንያቱም የእነርሱ የሥራ ድርሻ የያህዌ የሆኑትን ነገሮች በገዛ ትከሻቸው ከመሸከም ጋር የተያያዘ ነው፡፡ 10 መሪዎቹ ሙሴ መሰዊያውን በቀባ ዕለት ስጦታዎቻቸውን ለመሰዊያው መቀደስ ሰጡ፡፡ መሪዎቹ መስዋዕቶቻቸውን በመሰዊያው ፊት አቀረቡ፡፡ 11 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “እያንዳንዱ መሪ ለመሰዊያው መቀደስ በራሱ ቀን መስዋዕቱን ማቅረብ አለበት፡፡” 12 በመጀመሪያው ቀን፣ ከይሁዳ ጎሳ የሆነው፣ የአሚናዳብ ልጅ ነአሶን፣ መስዋዕቱነ አቀረበ፡፡ 13 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሳህን ነበሩ፡፡ እነዚህ ሁለትም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 14 በተጨማሪም በእጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሃን ሰጠ፡፡ 15 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ፣ እና የአንድ አመት ወንድ ጠቦት በግ ሰጠ፡፡ 16 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 17 ሁለት በሬዎች፣ አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ የበግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የአሚናዳብ ልጅ የነአሶን መስዋዕት ነበር፡፡ 18 በሁለተኛው ቀን፣ የይሳኮር መሪ፣ የሶገር ልጅ ናትናኤል፣ መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 19 አንድ መቶ ሰላሳ ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 20 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 21 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 22 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 23 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የሶገር ልጅ የናትናኤል መስዋዕት ነበር፡፡ 24 በሶስተኛው ቀን የዛብሎን መሪ፣ የኬሎን ልጅ ኤልያብ፣ መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 25 አንድ መቶ ሰላሳ ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 26 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 27 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 28 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 29 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የኬሎን ልጅ የኤልያብ መስዋዕት ነበር፡፡ 30 በአራተኛው ቀን፣ የሮቤል ትውልድ መሪ የሰዲዮር ልጅ ኤሊሱር መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 31 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 32 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 33 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 34 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 35 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የሰዲዮር ልጅ የአሌሊሱር መስዋዕት ነበር፡፡ 36 በአምስተኛው ቀን፣ የስምዖን ትውልድ መሪ፣ የሱሪሰዳይ ልጅ ስልሚኤል መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 37 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 38 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ። 39 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 40 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 41 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የሱሪሰዳይ ልጅ የስልሚኤል መስዋዕት ነበር፡፡ 42 በስድስተኛው ቀን፣ የጋድ ትውልድ መሪ፣ የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 43 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 44 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 45 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 46 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 47 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የራጉኤል ልጅ የኤሊሳፍ መስዋዕት ነበር፡፡ 48 በሰባተኛው ቀን፣ የኤፍሬም ትውልድ መሪ፣ የዓመሁድ ልጅ ኤሊሳማ መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 49 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 50 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 51 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 52 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 53 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የራጉኤል ልጅ የኤሊሳፍ መስዋዕት ነበር፡፡ 54 በስምንተኛው ቀን፣ የምናሴ ትውልድ መሪ፣ የፍደሱር ልጅ ገሚልኤል መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 55 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 56 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 57 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 58 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 59 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የፍደሱር ልጅ የገማልኤል መስዋዕት ነበር፡፡ 60 በዘጠነኛው ቀን፣ የብንያም ትውልድ መሪ፣ የጋዴዮን ልጅ አቢዳን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 61 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 62 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 63 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 64 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 65 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የጋዲዮን ልጅ የአቢዳን. መስዋዕት ነበር፡፡ 66 በአስረኛው ቀን፣ የዳን ትውልድ መሪ፣ የአሚሳይ ልጅ አኪዔዘር መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 67 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 68 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 69 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 70 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 71 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የፍደሱር ልጅ የገማልኤል መስዋዕት ነበር፡፡ 72 በአስራ አንደኛው ቀን፣ የአሴር ትውልድ መሪ፣ የኤክራን ልጅ ፋግኤል መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 73 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 74 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 75 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 76 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 77 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የኤክራን ልጅ የፋግኤል መስዋእት ነበር፡፡ 78 በአስራ ሁለተኛው ቀን፣ የንፍታሌም ትውልድ መሪ፣ የዔናን ልጅ ኢኬሬ መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ 79 መስዋዕቱ ይህ ነበር፣ በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 130 ሰቅሎችን የሚመዝን አንድ ሳህን እና ሰባ ሰቅሎች የሚመዝን አንድ ጎድጓዳ የብር ሰሀን በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን መስዋዕቱን አቀረበ፡፡ እነዚህ ሁለቱም ዕቃዎች ለእህል ቁርባን የሚሆን በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የተሞሉ ነበሩ፡፡ 80 በተጨማሪም በዕጣን የተሞላ አስር ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የወርቅ ሰሀን ሰጠ፡፡ 81 ለሚቃጠል መስዋዕት አንድ ኮርማ፣ አንድ አውራ በግ እና የአንድ አመት ወንድ በግ ጠቦት ሰጠ፡፡ 82 ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ሰጠ፡፡ 83 ሁለት በሬዎች አምስት አውራ በጎች፣ አምስት ወንድ ፍየሎች፣ እና አንድ አመት የሆናቸው አምስት ወንድ በግ ጠቦቶች፣ ለህብረት መስዋዕት ሆነው እንዲቀርቡ ሰጠ፡፡ ይህ የኤናን ልጅ የኤኪሬ መስዋዕት ነበር፡፡ 84 የእስራኤል መሪዎች ሙሴ መሰዊያውን በቀባበት ቀን እነዚህን ሁሉ ነገሮች አቀረቡ፡፡ አስራ ሁለት የብር ሳህኖች፣ አስራ ሁለት የብር ጎድጓዳ ሳህኖች እና አስራ ሁለት የወርቅ ሰሃኖች አቀረቡ፡፡ 85 እያንዳንዱ የብር ሳህን 130 ስቅሎች ሲመዝን እያንዳንዱ ጎድጓዳ ሰሀን ሰባ ሰቅሎች ይመዝናል፡፡ ሁሉም የውሃ መያዣዎች በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን 2400 ሰቅሎች ይመዝናሉ፡፡ 86 አስራ ሁለቱ ዕጣን የተሞሉ የወርቅ ሰሃኖች እያንዳንዳቸው በቤተ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን አስር ሰቅሎች ይመዝናሉ፡፡ ሁሉም የወርቅ ሳህኖች 120 ሰቅሎች ይመዝናሉ፡፡ 87 ለሚቃጠል መስዋዕት አስራ ሁለት በሬዎች፣ አስራ ሁለት አውራ በጎች፣ እና አስራ ሁለት የአንድ አመት ጠቦቶች አቀረቡ፡፡ የእህል ቁርባናቸውን ሰጡ፡፡ ለኃጢአት መስዋዕት አስራ ሁለት ወንድ ፍየሎች ሰጡ፡፡ 88 ከብቶቻቸው ሁሉ፣ ሀያ አራት በሬዎች፣ ስልሳ አውራ በጎች፣ ስልሳ ወንድ ፍየሎች እና አንድ አመት የሆናቸው ስልሳ ወንድ ጠቦት በጎች የህብረት መስዋዕት አድርገው አቀረቡ፡፡ እነዚህ ሁሉ መሰዊያውን ለመቀደስ በሚቀባበት ጊዜ የቀረቡ ስጦታዎች ናቸው፡፡ 89 ሙሴ ከያህዌ ጋር ለመነጋገር ወደ መገናኛው ድንኳን በገባ ጊዜ፣ ከእርሱ ጋር ሲነጋገር ድምጹን ሰማ፡፡ ያህዌ ከማስተሰርያ መክደኛ በላይ ሆኖ በቃል ኪዳን ታቦቱ ላይ፣ በሁለቱ ኪሩቤል መካከል ለእርሱ ተናገረ፡፡



Numbers 7:1

ሙሴ ማደሪያውን ፈፀመ

“ሙሴ ማደሪያውን መሥራቱን አጠናቀቀ”

የእሥራኤል አለቆች …አባቶቻቸው ቤቶች አለቆች

እነዚህ ሁለት ሐረጎች በተለያዩ መንገዶች ሁለት ተመሳሳይ የሆኑ ቡድኖችን ነው የሚገልፁት፡፡“የእሥራኤል አለቆች የሆኑትና በተመሳሳይ ሁኔታ አባቶች ቤቶች አለቆች የሆኑ” (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የአባቶች ቤቶች አለቆች

እዚህ ላይ የአባቶች ቤቶች መሪዎች “አለቆች”ተብለው ተጠርተዋል፡፡ “የአባቶቻቸው ቤቶች መሪዎች”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የሚካሄደውን ቆጠራ ይከታተሉ ነበር

“ቆጠራ”የሚለው አሕፅሮተ ስም እንደ ግሥ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አሮንንና ሙሴን በቆጠራ አግዘዋቸዋል”(አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

መባቸውን በእግዚአብሔር ፊት አቀረቡ …ይህንንም በመገናኛው ድንኳኑ ፊት አቀረቡት

ይሄ ማለት መባቸውን ከሰጡ በኋላ ወደ መገናኛ ድንኳኑ አመጡት ማለት ነው፡፡ምናልባትም እነዚህ ሐረጎች ነገሩን የበለጠ ግልፅ ለማድረግ ሊቀናጁ ይችላሉ፡፡“መባቸውን ለእግዚአብሔር ካመጡ በኋላ በመገናኛ ድንኳኑ ፊት አቀረቡት፡፡”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ስድስት የተከደኑ ሠረገሎችና አሥራ ሁለት በሬዎች(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

6 የተከደኑ ሠረገሎችና 12 በሬዎች

Numbers 7:4

ለእያንዳንዱ እንደየገልግሎታቸው

“ለእንዳንዱ ለሥራው እንደሚያስፈልገው መጠን”

Numbers 7:6

ጌድሶን … ሜራሪ

ይሀንን በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

እንደ አገልገሎታቸው መጠን

“ምክኒያቱም ለሥራ የሚያስፈልጋቸውን ያህል ነበር”

ከካህኑም ከአሮን እጅ ከኢታምር በታች

“በካህኑ በአሮን ልጅ በኢታምር ተቆጣጣሪነት”ወይም “የካህኑ የአሮን ልጅ የሆነው ኢታምር ሥራቸውን ተመለከተ”

ኢታምር

ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የሚያደርጉት አገልግሎት በሚጠይቀው አንፃር

“ምክኒያቱም ሥራውን ለማከናወን የሚያስፈልጋቸው ይሄ ስለነበር”

Numbers 7:9

ከእነዚያ ነገሮች አንዱ እንኳን

ይሄ የሚያመለክተው ሠረገሎቹንና በሬዎቹን ነው፡፡

ቀአት

ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ማገልገል የእነርሱ ነውና

“ሥራቸው የሚሆነው”

ለእግዚአብሔር የሆኑት ዕቃዎች

ለእግዚአብሔር የሆኑት ነገሮች የሚለውንና በአግባቡ ያልተገለፀውን ነገር በሚገባ ልትገልፁት ትችላላችሁ፡፡“ እግዚአብሔር ለመገናኛ ድንኳኑ እንዲሆን የመደበው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:10

ዕቃዎቻቸውን አቀረቡ

“ሥጦታዎችን አቀረቡ”

እያንዳንዱ አለቃ መሥዋዕቱን በተመደበለት ቀን ማቅረብ ይጠበቅበታል

“አንድ መሪ በእያንዳንዱ ዕለት መሥዋዕቱን ማቅረብ ይኖርበታል”

Numbers 7:12

በመጀመሪያው ቀን

“ቀን 1”ወይም “ቀን ቁጥር 1” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የአሚናዳብ ልጅ ነአሶን

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅል የሚመዝን

“አንድ መቶ ሠላሣ ሰቅል የሚመዝን” “አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ክብደቶች በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፉ ይችላሉ፡፡” “አንድ ኪሎ ግራም አካባቢ የሚመዝን”ወይም “አንድ ኪሎ ግራምና 430 ግራሞች” (ቁጥሮችንና የመፅሐፍ ቀዱስ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሆነ አንድ የብር ድስት

“ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብረት ድስት”አስፈላጊ የሚሆን ከሆነ እነዚህን መመዘኛዎች በዘመናዊ መለኪያ መለካት ይችላል፡፡“አንድ አስረኛ ኪሎግራም አካባቢ የሚመዝን”ወይም “770 ግራም የሚመዝን አንድ የብረት ድስት”

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡ሚዛኖቹን ወደ ዘመናዊ መለኪያ እየለወጣችሁ ከሆነ ይሄንን ሐረግ የመተርጎሚያ ሌላ መንገድ እነሆ፡፡“በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የሚዛን ደረጃ የተለካ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ) “እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

የአሚናዳብ ልጅ የነአሶን መባ ይሄ ነበረ

ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:18

በሁለተኛውም ቀን

“ቀን 2”ወይም “ቀን ቁጥር 2” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የሶገር ልጅ ናትናኤል

ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናሉል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን ሰዎች የሚጠቀሙበት ነው፡፡ሚዛኖቹን ወደ ዘመናዊ መለኪያ እየለወጣችሁ ከሆነ ይሄንን ሐረግ የመተርጎሚያ ሌላ መንገድ እነሆ፡፡“በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው ደረጃ ሚዛን የተለካ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡” በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:20

አሥር ሰቅሎች የሚመዝን የወርቅ ሰሃን

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የወርቅ ሳህን አንድ አሥረኛ ኪሎ ግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሳህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የሶገር ልጅ የናትናኤል መሥዋዕት ነው

“ይሄ የሶገር ልጀ ናትናኤል ያቀረበው ነው”

የሶገር ልጅ ናትናኤል

የዚህን ሰው ስም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:24

በሶስተኛውም ቀን

“ቀን 3”ወይም “ቀን ቁጥር 3” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የኬሎን ልጅ ኤልያብ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናሉ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የጥራት ደረጃ መሠረት የተመዘነ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡” በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:27

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የኬሎን ልጅ የኤልያብ መሥዋዕት ነው

“የኬሎን ልጅ ኤልያብ ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የኬሎን ልጅ ኤልያብ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡19 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:30

በአራተኛውም

“ቀን 4”ወይም “ቀን ቁጥር 4” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የሰዲዮር ልጅ ኤሊሱር

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የጥራት ደረጃ መሠረት የተመዘነ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡” በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን እንዴት በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎ ግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:33

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የሰዲዮር ልጅ ኤሊሱር መሥዋዕት ነው

“የሰዲዮር ልጅ ኤሊሱር ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የኬሎን ልጅ ኤልያብ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:36

በአምስተኛውም ቀን

“ቀን 5”ወይም “ቀን ቁጥር 5” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የሱሪሰዳይ ልጅ ሰለሚኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን ሰዎች የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው ደረጃ ሚዛን የተለካ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡” በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን እንዴት በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:39

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የሱዲዮር ልጅ የሰለሚኤል መሥዋዕት ነው

“የሱዲዮር ልጅ ሰለሚኤል ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የሱዲዮር ልጅ ሰለሚኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:42

በስድስተኛውም ቀን

“ቀን 6”ወይም “ቀን ቁጥር 6” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው ደረጃ ሚዛን የተለካ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን እንዴት በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:45

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የራጉኤል ልጅ የኤሊሳፍ መሥዋዕት ነው

“የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:48

በሰባተኛውም ቀን

“ቀን 7”ወይም “ቀን ቁጥር 7” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የዓሚሁድ ልጅ ኤሊሳማ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡10 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የጥራት ደረጃ መሠረት የተመዘነ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:51

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የአሚሁድ ልጅ የኤሊሳማ መሥዋዕት ነው

“የአሚሁድ ልጅ ኤሊሳማ ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

Numbers 7:54

በስምንተኛውም ቀን

“ቀን 8”ወይም “ቀን ቁጥር 8” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የፍዳሱር ልጅ ገማልኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡10 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው ደረጃ ሚዛን የተለካ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:57

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የፍሳዱል ልጅ የገማልኤል መሥዋዕት ነው

“የፍሳዱል ልጅ ገማልኤል ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የፍሳዱል ልጅ ገማልኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:60

በዘጠነኛውም ቀን

“ቀን 9”ወይም “ቀን ቁጥር 9” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የጋዴዮን ልጅ አቢዳን

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን ሰዎች የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የጥራት ደረጃ መሠረት የተመዘነ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎ ግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:63

አንድ ዓመት የሆነው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የአቢዳን ልጅ የጋዴዮን መሥዋዕት ነው

“የአቢዳን ልጅ ጋዴዮን ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የአቢዳን ልጅ ጋዴዮን

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:66

በአስረኛውም ቀን

“ቀን 10”ወይም “ቀን ቁጥር 10” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የአሚሳዳይ ልጅ አኪዔዘር

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡12 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው ደረጃ ሚዛን የተለካ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን እንዴት በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ የወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:69

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የአሚሳዳይ ልጅ የአኪዔዜር መሥዋዕት ነው

“የአሚሳዳይ ልጅ አኪዔዜር ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የአሚሳዳይ ልጅ አኪዔዜር

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡12 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:72

በአሥራ አንደኛውም ቀን

“ቀን 11”ወይም “ቀን ቁጥር 11” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የኤክራን ልጅ ፋግኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ 430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን ሰዎች የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የጥራት ደረጃ መሠረት የተመዘነ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:75

አንድ ዓመት የሆናቸው

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የኤክራን ልጅ የፋግኤል መሥዋዕት ነው

“የኤክራን ልጅ ፋግኤል ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡” ኤክራንና ፋግኤል የሰዎች ሥም ነው፡፡ስማቸውን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:78

በአሥራ ሁለተኛውም ቀን

“ቀን 12”ወይም “ቀን ቁጥር 12” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የዔናን ልጅ አኪሬ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ 430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሰቅል የሚመዝን አንድ የብር ድስት

“አንድ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”አንድ የብር ሣህን አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ሣህን 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን ሰዎች የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የጥራት ደረጃ መሠረት የተመዘነ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡”በዘይት የተለወሰው መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥር ሰቅል የሚመዝን አንድ የወርቅ ሣህን

አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ይሄ በዘመናዊ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡እነዚህን ተመሳሳይ የሆኑ ሚዛኖችን እንዴት በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመለከቱ፡፡”አንድ ወርቅ ሣህን አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝናል”ወይም “አንድ የወርቅ ሣህን 110 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:81

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

“እያንዳንዳቸው አንድ ዓመት የሆናቸው”

ይሄ የዔናን ልጅ የአኪሬ መሥዋዕት ነው

“የዔናን ልጅ አኪሬ ያቀረበው መሥዋዕት ይሄ ነበር፡፡”

የዔናን ልጅ አኪሬ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 7:84

እነዚህን ሁሉ ለዩልኝ

“መለየት”የሚለው ሐረግ ለአንድ ለተወሰነ ዓላማ ራስን መሥጠት ማለት ነው፡፡በዚህ መሠረት ሥጦታዎቹ የሚሰጡት ለእግዚአብሔር ነበር፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሙሴ መሠዊያውን በቀባበት ቀን

እዚህ ላይ“ቀን” የሚለው ቃል የሚያመለክተው በአጠቃላይ ዘመኑን ነው፡፡የእሥራኤል አለቆች እነዚህን ነገሮች በአሥራ ሁለት ቀናት ነበር የሚሰውት፡፡ “ሙሴ መሠውያውን በቀባበት ወቅት”

130 ሰቅሎች የሚመዝን አንድ የብር ወጭት

አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝ ከሆነ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች መፃፍ ይኖርባቸዋል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“አንድ የብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ተኩል ገደማ ይመዝናል”ወይም “አንድ ብር ወጭት አንድ ኪሎ ግራም ከ 430 ግራሞች ይመዝናል”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

እያንዳንዱ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝን ነበር

“እያንዳንዱ የብር ድስት 70 ሰቅል ይመዝን ነበርይመዝናል”አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላል፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”እያንዳንዱ የብር ድስት አንድ አሥራ ስምንተኛ ኪሎግራም ገደማ የሚመዝን ነው”ወይም “አንድ የብር ድስት 770 ግራም ይመዝናል፡፡”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

2,400 ሰቅል

“ሁለት ሺህ አራት መቶ ሰቅል”ወይም “ሃያ አራት መቶ ሰቅል”

በቤተመቅደሱ የሰቅል ሚዛን መሠረት

የተለያዩ ዓይነት የሰቅል ሚዛኖች ነበሩ፡፡ይሄኛው ሰዎች በመቅደሱ ውስጥ ለሚገኘው የተቀደሰው ድንኳን የሚጠቀሙበት ነው፡፡“ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡በመቅደሱ ውስጥ በሚገኘው የጥራት ደረጃ መሠረት የተመዘነ”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለከያ የሚለውን ይመልከቱ)

የብር ዕቃዎቹ ሁሉ ተመዘኑ…የወርቅ ዕቃዎቹ ሁሉ ተመዘኑ

“የብር ዕቃዎቹ ሁሉ በአንድ ላይ ተመዘኑ…የወርቅ ዕቃዎቹ ሁሉ በአንድ ላይ ተመዘኑ”

የብር ዕቃዎቹ ሁሉ

እነዚህ የሚያመለክቱት ከብር የተሰሩትን በሳህንና በወጭት መልክ የመጡትን ሥጦታዎች ነው፡፡

እንዳንዳቸው አሥራ ሁለቱ የወርቅ ሣህኖች …አሥር ሰቅል ይመዝኑ ነበር

“እንዳንዳቸው አሥራ ሁለቱ የወርቅ ሣህኖች …10 ሰቅል ይመዝኑ ነበር፡፡አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚህ ሚዛኖች በዘመናዊ መለኪያዎች ሊፃፉ ይችላሉ፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 7፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡”እያንዳንዳቸው 12 የወርቅ ሣህኖች…. አንድ አሥረኛ ኪሎግራም ይመዝኑ ነበር”ወይም “እንዳንዳቸው 12ቱ የወርቅ ሣህኖች 110 ግራም ይመዝኑ ነበር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

120 ሰቅል

“አንድ መቶ ሃያ ሰቅል” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:87

አሥራ ሁለት…ሃያ አራት..ስድሳ

“12..24…60”እነዚህ ቁጥሮች ከፊደል ይልቅ በቁጥር ሊፃፉ ይችሉ ይሆናል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

አንድ ዓመት

“አንድ ዓመት የሆነው”

ከተቀባ በኋላ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴ ከቀባው በኋላ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 7:89

የእርሱን ድምፅ ሲናገረው ሰማ

“የእርሱ”የሚለው የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ድምፅ ነው፡፡“እግዚአብሔር ሲናገረው ሰማ” (ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

ከሥርየት መክደኛ በላይ …ከኪሩቤልም መካከል

እነዚህ ሁለት ሐረጎች የሚያመለክቱት ተመሳሳይ የሆነን ሥፍራ ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የምሥክሩ ታቦት

ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 4፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

እርሱ ተናገረው

“እግዚአብሔር ለሙሴ ተናገረው”


Chapter 8

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “አሮንን እንዲህ በለው፣ ‘ሰባቱ መብራቶች በምትለኩሳቸው ጊዜ በመቅረዙ ፊት ለፊት ብርሃን ይስጡ፡፡’” 3 አሮን ይህን አደረገ፡፡ ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው፣ ከመቅረዙ ፊት ለፊት ብርሃን እንዲሰጡ መብራቶቹን በመቅረዙ ላይ ለኮሳቸው፡፡ 4 መቅረዙ የተሰራው በዚህ መንገድ ነበር፡፡ ያህዌ አሰራሩን ለሙሴ አሳይቶት ነበር፡፡ ከመሰረቱ እስከ ጫፍ በአበባ መልክ የዋንጫ መልክ ቅርጽ አስይዘህ ወርቁን ቀጥቅጠህ አብጀው፡፡ 5 እንደገና፣ ያህዌ ሙሴን እንዲሀ ሲል ተናገረው፣ 6 “ከእስራኤል ሰዎች መሃል ሌዋውያንን ወስደህ አንጻቸው፡፡ 7 እነርሱን ለማንጻት ይህን አድርግ፣ የማንጻት ውሃ እርጫቸው፡፡ ፀጉራቸው በሙሉ እንዲላጩ፣ ልብሶቻቸውን እንዲያጥቡ፣ እና በዚህ መንገድ ራሳቸውን እንዲያነጹ አድርግ፡፡ 8 ከዚያ ጥጃና በዘይት የተለወሰ የመልካም ዱቄት የእህል ቁርባን ይውሰዱ፡፡ ሌላ ጥጃ ለኃጢአት መስዋዕት ያዘጋጁ፡፡ 9 ሌዋውያኑን ወደ መገናኛው ድንኳን ፊት ለፊት አቅርባቸውና መላውን የእስራኤል ማህበረሰብ ሰብስብ፡፡ 10 በእኔ በያህዌ ፊት ሌዋውያንን አቅርብ፡፡ የእስራኤል ሰዎች እጃቸውን በሌዋውያን ላይ ይጫኑ፡፡ 11 አሮን ሌዋውያኑን በእኔ ፊት ያቅርባቸው፣ የእስራኤልን ህዝብ ወክለው በእርሱ ፊት ከፍ አድርገው እንደሚያቀርቡ አቅርባቸው፡፡ ሌዋውያን እኔን እንደሚያገለግሉ እርሱ ይህን ያድርግ፡፡ 12 ሌዋውያኑ በበሬዎቹ ላይ እጃቸውን ይጫኑ፡፡ ሌዋውያኑን ለማስተሰርይ፣ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ኮርማ አቅርቡ፣ ደግሞም ሌላውን ኮርማ የሚቃጠል መስዋዕት አድርገህ ለእኔ አቅርብ፡፡ 13 ሌዋውያኑን በአሮንና በልጆቹ ፊት አቁማቸው፣ እናም እንደ ሚወዘወዝ መሥዋዕት ለእኔ ከፍ አድርገህ አቅርባቸው፡፡ 14 በዚህ መንገድ ሌዋውያኑን ከእስራኤል ሰዎች መሃል ለያቸው፡፡ ሌዋውያን ለእኔ ይለዩ፡፡ 15 ከዚያ በኋላ ሌዋውያኑ ወደ መገናኛው ድንኳን ለአገልግሎት ይግቡ፡፡ እነርሱን አንጻቸው፡፡ እንደ ስጦታ ለእኔ ከፍ አድርገህ አንሳቸው፡፡ 16 ከእስራኤል ህዝብ መሀል እነርሱ ሙሉ ለሙሉ የእኔ ናቸውና ይህን አድርግ፡፡ ከእስራኤል ወገን በኩር ሁሉ፣ ማህጸን ከከፈተው ከእያንዳንዱ ወንድ ልጅ ቦታውን ይወስዳሉ፡፡ እኔ ሌዋውያንን ለራሴ ለይቻለሁ፡፡ 17 ከሰውም ሆነ ከእንስሳው የእስራኤል ህዝብ በኩሩ ሁሉ የእኔ ነው፡፡ በግብፅ ምድር የበኩሩን ህይወት ሁሉ በወሰድኩ ቀን፣ እኔ እናንተን ለራሴ ለየኋችሁ፡፡ 18 በበኩሩ ሁሉ ምትክ፣ ከእስራኤል ሰዎች መሀል ሌዋውያንን ወሰድኩ፡፡ 19 ሌዋውያንን ለአሮንና ለልጆቹ እንደ ስጦታ ሰጠኋቸው፡፡ በመገናኛው ድንኳን የእስራኤልን ሰዎች ሥራ ይስሩ ዘንድ ከእስራኤል ሰዎች መሃል ወሰድኳቸው፡፡ ወደተቀደሰው ስፍራ ሲቀርብ ምንም ጥፋት እንዳይደርስባቸው ለእስራኤል ሰዎች እንዲያስተሰርዩ እነርሱን ሰጠኋቸው፡፡” 20 ሙሴ፣ አሮንና መላው የእስራኤል ህዝብ ይህንን ከሌዋውያን ጋር አደረጉ፡፡ ሌዋውያንን በሚመለከት ያህዌ ሙሴን ያዘዘውን ነገር ሁሉ አደረጉ፡፡ የእስራኤል ሰዎች ከእነርሱ ጋር ይህን አደረጉ፡፡ 21 ሌዋውያን ልብሶቻቸውን በማጠብ ራሳቸውን ከኃጢአት አነጹ፡፡ አሮን ለያህዌ ስጦታ አድርጎ አቀረባቸው፤ ደግም ይነጹ ዘንድ የንስሃ ማስተስረያ አደረገላቸው፡፡ 22 ከዚያ በኋላ፣ ሌዋውያኑ በአሮንና በአሮን ልጆች ፊት አገልግሎታቸውን ይሰጡ ዘንድ ወደ መገናኛው ድንኳን ገቡ፡፡ ይህም ያህዌ ስለ ሌዋውያን ሙሴን ባዘዘው መሠረት ነበር፡፡ ሌዋውያንን በሙሉ በዚህ መንገድ ተቀበሉ፡፡ 23 ያህዌ እንደገና ለሙሴ ተናገረ፡፡ እንዲህም አለ፣ 24 “ይህ ሁሉ፤ ሃያ አምስት አመት እና ከዚያ በላይ ዕድሜ ላላቸው ሌዋውያን ነው፡፡ በመገናኛው ድንኳን ለማገልገል መምጣት አለባቸው፡፡ 25 አምሳ አመት ሲሞላቸው በዚህ መንገድ ማገልገላቸውን ያቁሙ፡፡ በዚያ ዕድሜ መደበኛ አገልግሎታቸውን ያቁሙ፡፡ 26 በመገናኛው ድንኳን የሚያገለግሉ ወንድሞቻቸውን ሊያግዙ ይችላሉ፣ ነገር ግን ዕድሜያቸው አምሳ ከሆነ በኋላ በዚህ መንገድ አያገለግሉ፡፡ ለሌዋውያን በእነዚህ ጉዳዮች ሁሉ መመሪያ ልትሰጣቸው ይገባል፡፡



Numbers 8:1

በፊቱ መብራት ማብራት ያስፈልጋል

“በመቅረዙ ፊት ያበራሉ”

Numbers 8:3

ብርሃን መሥጠት

“ማብራት”

የመቅረዙ ማስቀመጫ ተሰራ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የመቅረዙን ማስቀመጫ ሰሩት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ አበቦቹ ድረስ ከተቀጠቀጠ ሥራ

ከአፈራው አበባ ጋር እንዲመሳሰሉ የተቀጠቀጡ ፅዋዎችን እንዲቀርፁ ይታዘዙ ነበር፡፡“ከአበቡት አበባዎች ጋር እንዲመሳሰሉ የተቀጠቀጡ ፅዋዎች”(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 8:7

እነርሱን ሊቀድሳቸው

እዚህ ላይ “እነርሱን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሌዋውያንን ነው፡፡

ኃጢአትን የሚያነፃውን ውኃ እርጫቸው

ሙሴ በእነርሱ ላይ ውኃ መርጨቱ የድነታቸው ተምሣሌት ነው፡፡“የደህንነት ተምሣሌት የሆነውን ውኃ በእነርሱ ላይ መርጨት”(ተምሳሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

ልብሣቸውን ማጠብ

ሌዋውያን የራሣቸውን ልብስ ማጠብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ግንዛቤ የተገኘበትን ይህንን ሃሣብ የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡“ልብሣቸውን እንዲያጥቡ አድርግ”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

ልብሣቸውን ማጠብ

ሌዋውያን የራሣቸውን ልብስ ማጠብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ግንዛቤ የተገኘበትን ይህንን ሃሣብ የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡“ልብሣቸውን እንዲያጥቡ አድርግ”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

ወይፈንና የእህሉ ቁርባን

የወይፈን ሥጦታ በሚቀርብበት ወቅት አብዛኛውን ጊዜ የእህል ሥጦታም አብሮ ይሰጥ ነበር፡፡

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሱት መልካም ዱቄት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 8:9

ማህበሩን ሁሉ ሰብስብ

“ማህበሩን ሁሉ አንድ ላይ አድርጋቸው”

በእግዚአብሔር ፊት

እዚህ ላይ እግዚአብሔር የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔር ራሱን የሚገልፅበት ሥሙን ነው፡፡

የእሥራኤል ልጆች በሌዋውያን ላይ እጃቸውን መጫን ይኖርባቸዋል

አብዛኛውን ጊዜ በአንድ ሰው ላይ“ እጅ የመጫን” ድርጊት የሚከናወነው አንድ ሰው ለእግዚአብሔር ቤት ሥራ ወይም አገልግሎት በሚለይበት ወቅት ነው፡፡ለእኔ ይለዩ ዘንድ የእሥራኤል ሕዝብ በሌዋውያን ላይ እጃቸውን መጫን ይኖርባቸዋል፡፡(ተምሳሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

እንደሚወዘወዝ ሥጦታ

አሮን ሌዋውያንን ለእግዚአብሔር የሚያቀርባቸው መሥዋዕቶችን በሚያቀርብበበት ስሜት ውስጥ ሆኖ ነው፡፡“የሚወዝወዝ ሥጦታ እንደሆኑ”(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 8:12

ሌዋውያኑም በወይፈኖቹ ራሶች ላይ እጃቸውን መጫን ይኖርባቸዋል

ይሄ ተምሣሌታዊ አነጋገር ሲሆን ለሌዋውያን የከብቶች ሥጦታ እንደሚሰጣቸው ለመግለፅ ነው፡፡በዚህ መንገድ ሰውዬው በእንስሳው አማካይነት ራሱን ለእግዚአብሔር ያቀርባል፡፡(ተምሳሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

እንደሚወዘወዝ ሥጦታ አድርገህ ለእኔ አቅርባቸው

አሮን ቁርባንን እንደሚያነሳ እንዲሁ ሌዋውያንን በእግዚአብሔር ፊት ማቅረብ ነበረበት፡፡ “የሚወዘወዝ ቁርባንን እንደምታቀርብልኝ እንዲሁ እነርሱን ለእኔ ለይልኝ”

Numbers 8:14

ታነፃቸዋለህ፡፡ሥጦታም አድርገህ ታቀርባቸዋለህ፡፡

እግዚአብሔር እነዚህን ነገሮች የሚደጋግመው ለጉዳዩ አፅንዖትን ለመስጠት ነው፡፡ይሄ መከናወን የሚኖርበት ሌዋውያኑ በመገናኛ ድንኳን ውስጥ አገልግሎትን ከመጀመራቸው አስቀድሞ ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ነገር ግን በመጀመሪያ ልታነጿቸው ይገባል፡፡እንደ ሥጦታ ልታቀርቧቸው ይገባችኋል (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

እንደሚወዘወዝ ሥጦታ አድርገህ ታቀርባቸዋለህ

የሚወዘወዙ ቁርባን ይመስል አሮን እነርሱን ለእግዚአብሔር ማቅረብ ነበረበት፡፡“የሚወዘወዝ ቁርባን ለእኔ እንደሚቀርብ እንዲሁ እነርሱን ለእኔ ማቅረብ ይኖርብሃል፡፡”(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 8:16

በኩራት ሁሉ፤ማሕፀን የሚከፍት ሁሉ

በመሠረቱ እነዚህ ሁለቱ ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን በጋራ እንዲነገሩ የተደረገው በኩር ልጆችን በተመለከተ የበለጠ አፅንዖት ለመስጠት ሲባል ነው፡፡ (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ማሕፀንን የሚከፍት ወንድ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“ማሕፀንን የሚከፍት” ማለት ለመጀመሪያ ጊዜ ልጅን የሚወልድ ማለት ነው፡፡ይሄ የሚያመለክተው እናት ለመጀመሪያ ጊዜ የምትወልደውን ወንድ ልጅን ነው፡፡“ለእናቱ የመጀመሪያ ሆኖ የተወለደ ወንድ ልጅ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሕይወታቸውን ነጠቅኩ

ይሄ አንድ ሰው ሌላ ሰውን በሚገድልበት ወቅት የሚገለፅበት የትህትና አነጋገር ነው፡፡“ገደልኩ”(ሥርዓት የሌለውን ነገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱን ለእኔ ለይቻቸዋለሁ

እዚህ ላይ “እነርሱን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው “በእሥራኤል መካከል የተወለዱትን በኩሮች ነው”

Numbers 8:18

በበኩራቱ ፋንታ …ሌዋውያንን ወስጃለሁ

“ወስጃለሁ” የሚለው ቃል በመጀመሪያው ዓረፍተ ነገር ግልፅ ሲሆን በሁለተኛውም እንዲሁ ሊደገም ይችላል፡፡“በኩሮቹን ከመውሰድ ይልቅ…ሌዋውያንን በሙሉ ወስጃለሁ”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

ሌዋውያንን ለአሮንና ለልጆቹ ሥጦታ አድርጌ ሰጥቻቸዋለሁ

እግዚአብሔር ሌዋውያን አሮንና ልጆቹን እንዲያግዟቸው የመደበበትን ሁኔታ ልክ እግዚአብሔር ለአሮንና ለልጆቹ እንደ ሥጦታ እንደሰጣቸው ተደርጎ ሲነገር እናያለን፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱን ወስጃቸዋለሁ...እነርሱን ሰጥቻቸዋለሁ

እዚህ ላይ “እነርሱን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሌዋውያንን ነው፡፡

እነርሱ በሚቀርቡበት ወቅት

እዚህ ላይ “እነርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡

Numbers 8:20

ሙሴና አሮን የእሥራኤልም ማህበር ሁሉ…የእሥራኤል ማህበር ይህንን ከእነርሱ ጋር አደረጉ

እዚህ ላይ ተመሳሳይ መረጃ የሚሰጡ ሶስት ተመሳሳይ ዓረፍተ ነገሮች አሉ፡፡እንዲደጋገም የተፈለገበት ምክኒያት ሰዎቹ በሌዋውያን ላይ ያደረጉት ነገር በእግዚአብሔር ትዕዛዝ እንደሆነ አፅንዖት ለመሥጠት ነው፡፡ሙሴና አሮን የእሥራኤልም ማህበር ሁሉ ሌዋውያንን በሚመለከት እግዚአብሔር የሰጠውን ትዕዛዝ ሁሉ ፈፀሙ፡፡ (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 8:22

አገልግሎታቸውን ይሰሩ ዘንድ

“አገልግሎት”የሚለው አሕፅሮተ ሥም በግሥ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ማገልገል”(አሕፅሮተ ሥምን የሚለውን ይመልከቱ)

በአሮንና በልጆቹ ፊት

x

Numbers 8:25

ዕድሜያቸው ሃምሳ ዓመት ሲሞላ

“በሃምሳ ዓመት ዕድሜ” ወይም “ሃምሳ ዓመት ሲሞላቸው”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 9

1 ከግብጽ ምድር ከወጡ በኋላ በሁለተኛው አመት በመጀመሪያው ወር፣ በሲና ምድረ በዳ ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 2 “የእስራኤል ሰዎች በተወሰነው የአመቱ ወቅት ፋሲካን ያድርጉ፡፡ 3 በዚህ ወር በእስራ አራተኛው ቀን፣ ምሽት ላይ፣ በተወሰነው በአመቱ ወቅት ፋሲካን አድርጉ፡፡ ፋሲካን አድርጉ፣ ደንቦቹን ጠብቁ፣ ከዚህ ጋር የተያያዙ ደንቦችን ሁሉ ታዘዙ፡፡” 4 ስለዚህ፣ ሙሴ የፋሲካን በዓል እንዲያከብሩ ለእስራኤል ሰዎች ሁሉ ነገራቸው፡፡ 5 ስለዚህ በመጀመሪያው ወር በወሩ በአስራ አራተኛው ቀን፣ ምሽት ላይ፣ በሲና ምድረ በዳ ፋሲካን አከበሩ፡፡ የእስራኤል ሰዎች ያህዌ ለሙሴ እንዲያደርግ ያዘዘውን ሁሉ አደረጉ፡፡ 6 በሞተ ሰው በድን የረከሱ አንዳንድ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነርሱ በዕለቱ ፋሲካን አላከበሩም፡፡ በዚያ ቀን እነዚህ ሰዎች ሙሴና አሮን ፊት ቀረቡ፡፡ 7 እነዚያ ሰዎች ሙሴን እንዲህ አሉት፣ “እኛ በሰው በድን አካል ምክንያት ንጹህ አይደለንም፡፡ ሆኖም በእስራኤል ሰዎች መሃል በተወሰነው የአመቱ ወቅት ለያህዌ መስዋዕት ከማቅረብ ለምን ትከለክለናለህ” 8 ሙሴ እንዲህ አላቸው፣ “ያህዌ ስለ እናንተ ምን ትዕዛዝ እንደሚሰጥ እስከምሰማ ጠብቁኝ፡፡” 9 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 10 ”ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‘ከእናንተ ማናችሁም ወይም ከትውልዳችሁ ማንም በበድን አካል ምክንያት እርኩስ ቢሆን፣ ወይም ሩቅ መንገድ ሄዶ ቢሆን፣ ለያህዌ ፋሲካን ማክበር ይችላል፡፡’ 11 እነርሱ በሁለተኛው ወር በአስራ አራተኛው ቀን ፋሲካን ያክብሩ፡፡ እነርሱ ፋሲካን እርሾ ባስገባበት እንጀራ ከመራራ ቅጠል ጋር ይብሉ፡፡ 12 እስከ ማለዳ አንዳች አያስተርፉለት፣ አሊያም ከእንስሳቱ አጥንት አይስበሩ፡፡ የፋሲካን ህግጋት ሁሉ ይጠብቁ፡፡ 13 ነገር ግን ማናቸውም ንጹህ የሆነና ሩቅ መንገድ ያልሄደ ሰው፣ ነገር ግን ፋሲካን ሳያከብር የቀረ ሰው፣ ከህዝቡ ተለይቶ ይጥፋ፤ ምክንያቱም እርሱ በተወሰነው የአመቱ ወቅት የሚቀርበውን ያህዌ የሚጠይቀውን መስዋዕት አላቀረበም፡፡ ያሰው ኃጢአቱን ይሸከም፡፡ 14 እንግዳ በመሀላችሁ ቢኖርና ፋሲካን ለያህዌ ክብር ቢያብር፣ ፋሲካን መጠበቅና እርሱ ያዘዘውን ሁሉ ማድረግ አለበት፣ የፋሲካን ህግጋት ሁሉ መጠበቅ እንዲሁም የፋሲካን ህግነት መጠበቅ አለበት፡፡ ለመጻተኞች እና በምድሪቱ ለተወለዱ ሁሉ ተመሳሳይ ህግ ይኑርህ፡፡” 15 የማደሪያው ድንኳን በተተከለበት ቀን፣ ደመና የማደሪያውን ድንኳን ፣ የቃል ኪዳኑን ምስክር ድንኳን ሸፈነው፡፡ በምሽት ደመናው በማደሪያ ድንኳኑ ላይ ነበር፡፡ እስከ ንጋት እሳት ይመስል ነበር፡፡ 16 በዚያ መልክ ቀጠለ፡፡ ደመናው የማደሪያ ድንኳኑን ሸፍኖ በምሽት እሳት ይመስል ነበር፡፡ 17 ደመናው ከድንኳኑ ላይ በተወሰደ ጊዜ ሁሉ፣ የእስራኤል ሰዎች ከመጓዝ ያቋርጡ ነበር፡፡ ደመናው በቆመ ጊዜ ሁሉ፣ ህዝቡ አንድ ቦታ ይሰፍራል፡፡ 18 የእስራኤል ሰዎች በያህዌ ትዕዛዝ ይጓዛሉ፣ በእርሱም ትእዛዝ በሰፈራቸው ይቆያሉ፡፡ ደመናው በማደሪያው ድንኳን ላይ ሲቆም፣ በሰፈራቸው ይቆያሉ፡፡ 19 ደመናው በማደሪያው ድንኳን ለብዙ ቀናት ሲቆይ፣ የእስራኤል ሰዎች የያህዌን ትዕዛዝ ተከትለው መጓዝ ያቆማሉ፡፡ 20 አንዳንድ ጊዜ ደመናው በማደሪያው ድንኳን ላይ ለጥቂት ቀናት ይቆያል፡፡ በዚህ ሁኔታ የያዌን ትእዛዝ ተከትለው በአንድ ቦታ ይሰፍራሉ፣ ከዚያ በእርሱ ትእዛዝ እንደገና ይጓዛሉ፡፡ 21 አንዳንድ ጊዜ ደመናው ከምሽት እስከ ማለዳ በሰፈር ይገኛል፡፡ ማለዳ ደመናው ሲነሳ፣ እነርሱ ይጓዛሉ፡፡ ቀንም ይሁን ሌሊት ጉዟቸውን የሚቀጥሉት ደመናው ከተነሳ ብቻ ነው፡፡ 22 ደመናው በማደሪያ ድንኳኑ ላይ ለሁለት ቀናት፣ ለወር ወይም ለአመት ቢቆይ በዚያ ስፍራ እስከ ቆየ ድረስ የእስራኤል ሰዎች በሰፈሮቻቸው ይቆያሉ አይጓዙም፡፡ ነገር ግን ደመናው ሲንቀሳቀስ እነርሱም ጉዟቸውን ይቀጥላሉ፡፡ 23 በያህዌ ትዕዛዝ ይሰፍራሉ፣ በእርሱ ትዕዛዝ ይጓዛሉ በሙሴ በኩል የተሰጣቸውን የያህዌን ትዕዛዝ ይፈጽማሉ፡፡



Numbers 9:1

ከግብፅ ምድር በወጡ በሁለተኛው ዓመት በመጀመሪያው ወር

ይሄ ማለት ከግብፅ ምድር የወጡት ከአንድ ዓመት ቀደም ብሎ ነው ማለት ነው፡፡ሁለተኛ ዓመታቸውን እየጀመሩ የነበሩት በበረሃ ውስጥ ሆነው ሳሉ ነው፡፡(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

በመጀመሪያው ወር

በዕብራውያን የዘመን አቆጣጠር መሠረት ይሄ የመጀመሪያው ወር ነው፡፡እግዚአብሔር የእሥራኤልን ሕዝብ ከግብፅ ምድር ያወጣበትን ጊዜ የሚያመለክት ነው፡፡(የዕብራውያን ወራትንና ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱ ከግብፅ ምድር ከወጡ በኋላ

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡“ወጡ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው መልቀቅን ነው፡፡“የግብፅ ምድርን ከለቀቁ በኋላ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሕዝቡ…በተመደበው ዓመት ላይ ያድርጉት

“የተመደበው”የሚለው ቃል ቀደም ሲል መርሐ ግብር በተያዘለት መሠረት ማለት ነው፡፡ይሄ ማለት በየዓመቱ ይህን ያደርጋሉ ማለት ነው፡፡“ሕዝቡ…በዓመቱ በሚያከብሩት መሠረት” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በአሥራ አራተኛው ቀን…በተመደበው ዓመት

ይሄ ፋሲካን የሚያከብሩበት ዓመት ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ ሊብራራ የበለጠ ይችላል፡፡ “በአሥራ አራተኛው ቀን …አክብሩት፡፡በየዓመቱ ማክበር የሚኖርባችሁ በዚህ ወቅት ነው ነው” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አራተኛው ቀን

“ቀን 14” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ ሥርዓቱ ሁሉ እንደ ፍርዱም ሁሉ አድርጉት

በመሠረቱ እነዚህ ሁለቱ ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ሁለቱ እንዲቀናጁ የተደረጉት ትዕዛዙን መፈፀም የሚኖርባቸው ስለመሆኑ አፅንዖት ለመስጠት ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ልትጠብቁት ይገባል

“ልትጠብቁት”የሚለው ቃል ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን አክብሩት ማለት ነው፡፡ “ልታከብሩት ይገባል”ወይም “ትኩረት ልትሰጡት ይገባል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 9:4

የፋሲካን በዓል ጠብቁ

እዚህ ላይ “ጠብቁት” የሚለው ቃል ትርጉሙ አክብሩት ማለት ነው፡፡“ለፋሲካ በዓል ትኩረት ስጡ”ወይም “የፋሲካን በዓል አክብሩ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በመጀመሪያው ወር በአሥራ አራተኛው ቀን

“በመጀመሪያው ወር በ14ኛው ቀን” ይሄ የዕበራውያንን የዘመን አቆጣጠር ያሣያል፡፡(የዕብራውያን ወራትንና ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 9:6

በሞተ ሰው ሬሣ የረከሱ

ይሄ የሚያሣየው የሞተ ሰው ሬሣን ከመንካታቸው የተነሣ የረከሱ መሆናቸውን ነው፡፡የዚህን ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡“የሞተ ሰው ሬሣ ከመንካታቸው የተነሣ ረከሱ” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ንፁሕ ያልሆነ

እግዚአብሔር አንድን ሰው በመንፈሣዊ ሕይወቱ ተቀባይነት እንደሌለውና ወይም የረከሰ እንደሆነ የሚቆጥረውን ሰው እዚህ ሥፍራ ላይ ልክ ሰውነቱ ንፁህ እንዳልሆነ ተደርጎ ይገለፃል፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ፋሲካን ጠብቁ

“ጠብቁ”የሚለው ቃል ትኩረት ስጡት ማለት ነው፡፡ “ፋሲካን በአግባቡ ትኩረት ስጡት”ወይም “ፋሲካን አክብሩት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከሞተ ሰው ሬሣ የተነሣ

ይሄ ማለት የሞተ ሰው ሬሣ ነክተዋል ማለት ነው፡፡የዚህን ዓረፍተ ነገር ሙሉ ፍቺ ማብራራት ትችላላችሁ፡፡“የሞተ ሰው ሬሣ ከመንካታችን የተነሣ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሥራኤል መካከል ….መሥዋዕትን ከማድረግ የምታግደን ለምንድነው?

ሰዎቹ ይሄንን ጥያቄ የሚጠይቁት በፋሲካ በዓል ላይ እንዳይሳተፉ የተደረጉበትን ሁኔታ ቅሬታ ለማቅረብ ነወ፡፡ይሄ ምላሽ የማያሻው ጥያቄ በዓረፍተ ነገር መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእሥራኤል ሕዝብ መካከል ….ከመሥዋዕቱ ሥጦታ እኛን ማግለላችሁ ተገቢ አይደለም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

አቋም መያዝ

አቋም መያዝ ወይም አስቀድሞ መወሰን፡፡

Numbers 9:9

ንፁሕ ያልሆነ

እዚህ ሥፍራ ላይ እግዚአብሔር አንድን ሰው በመንፈሣዊ ሕይወቱ ተቀባይነት እንደሌለውና ወይም የረከሰ እንደሆነ የሚቆጥረውን ሰው ልክ ሰውነቱ ንፁህ እንዳልሆነ ተደርጎ ይገለፃል፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከሞተ ሰው ሬሣ የተነሣ

ይሄ ማለት የሞተ ሰው ሬሣ ነክተዋል ማለት ነው፡፡የዚህን ዓረፍተ ነገር ሙሉ ፍቺ የበለጠ ማብራራት ትችላላችሁ፡፡“የሞተ ሰው ሬሣ ከመንካታችን የተነሣ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ፋሲካን ጠብቁ

“ጠብቁ”የሚለው ቃል በአግባቡ አስቡት ማለት ነው፡፡ “ፋሲካን በአግባቡ አስቡት”ወይም “ፋሲካን አክብሩት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 9:11

በፋሲካ ብሉ

እዚህ ላይ “መብላት”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ማክበርን ነው፡፡“ለፋሲካ ትኩረት ሥጡ”ወይም “ፋሲካን አክብሩ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በሁለተኛው ወር በአሥራ አራተኛው ቀን

“14ኛ ቀን 2ተኛ ወር” ይሄ የአይሁዳውያንን የቀን አቆጣጠር የሚያመለክት ነው፡፡(የዕብራውያን ወራትንና ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

በመሸ ጊዜ

“ፀሐይ ስትገባ”

እርሾ ከሌለበት ቂጣ ጋር

“እርሾ የሌለው ቂጣ”

መራራ ቅጠሎች

እነዚህ ቅጠሎች ትናንሾች ሲሆኑ አብዛኛውን ጊዜ ጠንካራና መራራ ጣዕም ያላቸው ናቸው፡፡

ወይም ከእርሱም አጥንት አይስበሩ

“እና ከእርሱ ማንኛውንም እንት መስበር አይኖርባቸውም”

Numbers 9:13

ንፁህ የሆነ ማንኛውም ሰው

እዚህ ሥፍራ ላይ እግዚአብሔር አንድን ሰው በመንፈሣዊ ሕይወቱ ተቀባይነት እንዳለው የሚቆጥረውን ሰው ልክ ሰውነቱ ንፁህ እንደሆነ ተደርጎ ይገለፃል፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ፋሲካን ጠብቁ

“ጠብቁ”የሚለው ቃል ትኩረት ስጡት ማለት ነው፡፡ “ፋሲካን በአግባቡ ትኩረት ስጡት”ወይም “ፋሲካን አክብሩት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሰውዬው መቆረጥ ይኖርበታል

እዚህ ላይ “መቆረጥ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ንብረቱን መንጠቅና ማባረርን ነው፡፡ “ያ ሰው መባረር ይኖርበታል”ወይም “ያንን ሰው ማባረር ይኖርባችኋል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አቋም መያዝ

አቋም መያዝ ወይም አስቀድሞ መወሰን፡፡

ያ ሰው ኃጢአቱን መሸከም ይኖርበታል

እዚህ ላይ አንድ ሰው የኃጢአትን ውጤቶች መሸከም እንዳለበት የሚገልፀውን ሃሣብ ኃጢአቱን እንደ ዕቃ እንደሚሸከመው ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ያ ሰው የኃጢአቱን ቅጣት መሸከም ይኖርበታል”

በእናንተ መካከል ይኖራል

እዚህ ላይ “እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር ሲሆን የሚያመለክተውም የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡(እናንተ የሚለውን የተለያዩ አገላለፆች የሚለውንይመልከቱ)

ትዕዛዛቱን ሁሉ መጠበቅና ማድረግ ይኖርበታል

“ያ መፃተኛ ሰው እግዚአብሔር የሚያዝዘውን ትዕዛዛት መጠበቅና ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅበታል”

የፋሲካን ሥርዓት ይጠብቅና ሕጉን ይታዘዝ ዘንድ

በመሠረቱ እነዚህ ሁለቱ ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ሁለቱ ሐረጎች እንዲቀናጁ የተደረጉበት ምክኒያት መፃተኛው የፋሲካን ሕጎች በሙሉ መታዘዝ እንደሚኖርበት አፅንዖት ለመሥጠት ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

በምድሩ ውስጥ

“በእሥራኤል ምድር ውስጥ”

Numbers 9:15

ማደሪያው ተተከለ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሌዋውያን ማደሪያውን ተከሉ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለምሥክሩ ድንኳን የተቀመጡ ሥርዓቶች

ይሄ የመገናኛ ድንኳኑ ሌላ ሥም ነው፡፡“የምሥክሩ ድንኳን ሥርዓቶች የሚለውን ሐረግ ”በኦሪት ዘኁልቁ 1፡50 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

እስከ ማለዳ ድረስ እሣት ይመስል ነበር

ይሄ ደመናው በሌሊት የሚኖረውን ገፅታ የሚገልፅ ነው፡፡እዚህ ላይ ደመናው ከእሣት ጋር ሲመሳሰል እንመለከታለን፡፡“ሌሊት በሚሆንበት ወቅት ማለዳ እስኪነጋ ድረስ ደመናው ግዙፍ እሣት ይመስል ነበር” (ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

በዚሁ ሥርዓት መሠረት ይቀጥል ነበር

ደመናው ከመገኛና ድንኳኑ በላይ ይውል እንደነበረ መግለፁ ተገቢ ሊሆን ይችላል፡፡“ደመናው በዚህ መልኩ በመገናኛ ድንኳኑ ላይ ይቆይ ነበር” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በሌሊትም የእሣት አምሳል ይመስል ነበር

የደመናው አምሳል ከግዙፍ እሣት ጋር ተነፃፅሯል፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

ደመናው ይነሳ ነበር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ተንቀሳቀሰ” ወይም “እግዚአብሔር ደመናውን አነሳው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ደመናው ቆመ

“ደመናው መጓዙን አቋረጠ” “

Numbers 9:18

በእግዚአብሔር ትዕዛዝ መሠረት

“ትዕዛዝ”የሚለው ቃል እንደ ሥም (ሰዋሰው)ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በሚያዝበት ወቅት” (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 9:20

በማደሪያው ላይ

“ከማደሪያው በላይ”

ሠፈር ይሰሩ ነበር

እዚህ ላይ “መሥራት” የሚለው ቃል ማቋቋም ማለት ነው፡፡“ሠፈራቸውን ማቋቋም” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከማታ ጀምሮ እስከ ጥዋት ድረስ

ይሄ ማለት ደመናው በማደሪያው ላይ የሚቆየው ለአንድ ሊሊት ብቻ ነው ማለት ነው፡፡የዚህን ዓረፍተ ነገር ትርጉም የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡ “ከማታ ጀምሮ እስከ ጥዋት ድረስ ብቻ”ወይም “በማደሪያው ላይ ለአንድ ሌሊት ብቻ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የሚቀጥል ከሆነ

የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ደመናው በማደሪያው ላይ የሚቆይ ከሆነ” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ጉዞ የሚጀምሩት ደመናው ሲንቀሳቀስ ብቻ ነው

“ደመናው ሲንቀሳቀስ ጉዞ ይጀምራሉ”

Numbers 9:22

ደመናው ይነሣ ነበር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ደመናው ብድግ አለ”ወይም “እግዚአብሔር ደመናውን አነሳው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ትዕዛዝ

“ትዕዛዝ”የሚለው ቃል እንደ ግሥ ሊገለፅ ይችላል፡፡ (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

በሙሴ በኩል የተሰጠ የእግዚአብሔር ትዕዛዝ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በሙሴ በኩል የሰጠው ትዕዛዝ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 10

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 ”ሁለት የብር መለከቶች አብጁ፡፡ በብር ቀጥቅጠህ አብጃቸው፡፡ መለከቶቹን ማህበረሰቡን በጋራ ለመጥራትና ከመንደሮቸው እንዲንቀሳቀሱ ጥሪ ለማሰማት ተጠቀምባቸው፡፡ 3 ካህናቱ ማህበረሰቡን በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ በፊትህ ለመሰብሰብ መለኮቶቹን ይንፉ፡፡ 4 ካህናቱ አንድ መለከት ብቻ ከነፉ፣ የእስራኤል ነገድ መሪዎች ይሰበስቡ፡፡ 5 ከፍ ባለ ድምጽ ስትነፉ፣ በስተምስራቅ የሰፈሩት ጉዟቸውን ይጀምሩ፡፡ 6 ለሁለተኛ ጊዜ ከፍ ባለ ድምጽ ስትነፋ በደቡብ በኩል የሰፈሩት ጉዟቸውን ይጀምሩ፡፡ ለጉዟቸው ከፍ ያለ የመለከት ድምጽ ያሰሙ፡፡ 7 ማህበረሰቡ በአንድነት ሲበሰበሰብ፣ መለከቶች ይነፉ ነገር ግን ድምጹ ከፍ አይበል፡፡ 8 የካህኑ የአዘሮን ልጆች፣ መለኮቶቹን ይንፉ፡፡ በትውልዶቻችሁ ሁሉ ዘንድ ይህ ለእናንተ ሁልጊዜም ስርዓት ይሆናል፡፡ 9 በሚወሯችሁ ተቃዋሚዎቻች ላይ በምድራች ለጦርነት ስትወጡ፣ ለማንቂያ የመለከት ድምጽ ታሰማላችሁ፡፡ እኔ፣ አምላካችሁ ያህዌ፣ አስባችኋለሁ ደግሞም ከጠላቶቻችሁ አድናችኋለሁ፡፡ 10 እንደዚሁም፣ በመደበኛ ባዕላቶቻችሁም ሆነ በወራቶች መጀመሪያ ላይ በክብረ በዓል ወቅት ለሚቃጠል መስዋዕቶቻችሁ ክብርና በህብረት መስዋዕቶቻችሁ መስዋዕቶች ላይ መለኮቶችን መንፋት አለባች፡፡ እነዚህ እናንተ የእኔ የአምላካችሁ ለመሆናችሁ መታሰቢያ ሆነው ያገለግላሉ፡፡ እኔ አምላካችሁ ያህዌ ነኝ፡፡” 11 በሁለተኛው አመት፣ በሁለተኛው ወር፣ በወሩ ሀያኛ ቀን ደመናው ከቃል ኪዳኑ ምስክር ማደሪያ ላይ ተነሳ፡፡ 12 የእስራኤል ሰዎች ከሲና ምድረበዳ ተነስተው ጉዟቸውን ቀጠሉ፡፡ ደመናው በፋራን ምድረ በዳ ውስጥ ቆመ፡፡ 13 የመጀመሪያ ጉዟቸው፣ በሙሴ በኩል የተሰጣቸውን የያህዌን ትዕዛዝ ተከትለው አደረጉ፡፡ 14 በይሁዳ ትውልዶች ዓርማ ስር ያለው ሰፋሪዎች በመጀመሪያ ተንቀሳቀሱ፡፡ የይሁዳን ሠራዊት የሚመራው የአሚናዳብ ልጅ ነአሶን ነበር፡፡ 15 የይሳኮርን ትውልዶች ሰራዊት የሚመራው የሶገር ልጅ ናትናኤል ነበር፡፡ 16 የዛብሎንን ትውልዶች ሰራዊት የሚመራው የኬሎን ልጅ ኤልያብ ነበር፡፡ 17 የማደሪያ ድንኳኑን የተሸከሙት የጌድሶን እና የሜራሪ ትውልዶች፣ ማደሪያ ድንኳኑን ነቅለው ጉዟቸውን ጀመሩ፡፡ 18 ቀጥሎ፣ በሮቤል ሰፈር ሰራዊት ዓርማ ስር የነበሩት ጉዟቸውን ቀጠሉ፡፡ የሮቤልን ሰራዊት የሚመራው የሶዲዮር ልጅ ኤሊሱር ነበር፡፡ 19 የስምዖንን ትውልዶች ሰራዊት የሚመራዊ የሱሪስዓይ ልጅ ስለሚኤል ነበር፡፡ 20 የጋድን ትውልዶች ሰራዊት የሚመራው የራጉኤል ልጅ ኤሊሳፍ ነበር፡፡ 21 ቀዓታውያን ተነሱ፡፡ እነርሱ የቅድስተ ቅዱሳኑን ቅዱስ ዕቃዎች ተሸከሙ፡፡ ቀዓታውያን ቀጣዩ ሰፈር ከመድረሳቸው አስቀድሞ ሌሎች ማደሪያ ድንኳን ይተክላሉ፡፡ 22 የኤፍሬምን ሰራዊት የሚመራው የዓሚሁድ ልጅ ኤሊሳማ ነበር፡፡ 23 የምናሴን ትውልዶች ሰራዊት የሚመራው የፍዳሱር ልጅ ገማልኤል ነበር፡፡ 24 የብንያምን ትውልዶች ሠራዊት የሚመራው የጋዴዮን ልጅ አቢዳን ነበር፡፡ 25 በዳን ትውልዶች ዓርማ ስር የሰፈሩት ሠራዊቶች በመጨረሻ ይወጣሉ፡፡ የዳንን ሰራዊት የሚመራው የአሚሳዳይ ልጅ አኪዔዘር ነበር፡፡ 26 የአቤርን ትውልዶች ሰራዊት የሚመራው የኤክራን ልጅ ፋግኤል ነበር፡፡ 27 የንፍታሌምን ትውልዶች ሰራዊት የሚመራው የዔናን ልጅ አኪሬ ነበር፡፡ 28 የእስራኤል ሰዎች ሰራዊቶች ጉዟቸውን ያደረጉት በዚህ መልክ ነው፡፡ 29 ሙሴ ከምድያማዊው የራጉኤል ልጅ ከአባብ ጋር ተነጋገረ፡፡ ራጉኤል የሙሴ ሚስት አባት ነበር፡፡ ሙሴ ከአባብ ጋር ተነጋገረ እንዲህም አለ፣ “ያህዌ እሰጣችኋለሁ ወዳለን ስፍራ እየተጓዝን ነው፡፡ ያህዌ እንዲህ ብሎን ነበር፣ ‘እኔ ለእናንተ የተናገርኩትን እርሷኑ ስፍራ እሰጣችኋለሁ፡፡’ አንተ ከእኛ ጋር አብረኸን ና እኛም መልካም እናደርግልሃለን፡፡ ያህዌ ለእስራኤል መልካም ለማድረግ ቃል ገብቷል፡፡” 30 አባብ ግን ሙሴን እንዲህ አለው፣ “እኔ ከአንተ ጋር አልሄድም፡፡ እኔ ወደ ገዛ ምድሬና ወደ ራሴ ህዝብ እሄዳለሁ፡፡” 31 ከዚያም ሙሴ እንዲህ ሲል መለሰ፣ “እባክህን ከእኛ አትለይ፡፡ በበረሃ እንዴት መስፈር እንደሚቻል ታውቃለህ፡፡ ስንሰፍር ልትመለከተን ይገባል፡፡ 32 ከእኛ ጋር ብትሄድ፣ ያህዌ ለእኛ የሚያደርግልንን በጎነት ያንኑ እኛም ለአንተ እናደርግልሃለን፡፡” 33 ከያህዌ ተራራ ተነስተው ለሶስት ቀናት ተጓዙ፡፡ የያህዌ የቃልዳኑ ታቦት የሚያርፍበትን ስፍራ እንዲያገኙ ለመፈለግ ለሶስት ቀናት በፊታቸው ተጓዘ፡፡ 34 ሲጓዙ የያህዌ ደመና በቀን ብርሃን በላያቸው ነበር፡፡ 35 ታቦቱ በተነሳበት ጊዜ ሁሉ፣ ሙሴ እንዲህ ይላል፣ “ያህዌ ሆይ፣ ተነስ፡፡ ጠላቶችህን በትን፡፡ የሚጠሉህ ከአንተ እንዲሸሹ አድርግ፡፡” 36 ታቦቱ በቆመ ጊዜ ሁሉ፣ ሙሴ “ያህዌ ሆይ፣ ብዙ አስር ሺህ ወደሚሆኑት እስራኤላውያን ተመለስ” ይል ነበር፡፡



Numbers 10:1

ሁለት የብር መለከቶች

ይሄ ማለት እግዚአብሔር የሆነ ሰው መለከት እንዲሰራ ለሙሴ ትዕዛዝን ሰጥተታል ማለት ነው፡፡ራሱ አይደለም የሰራቸወ፡፡“ለአንድ ሰው ሁለት መለከቶቸን እንዲሰራ ንገረው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

መለከቶቹን ልትጠቀምባቸው ይገባሃል

ሙሴ መለከቶቹን የሚነፋው ራሱ ሳይሆን መለከቶቹን እንዲነፉ ካህናቱን ያዝዛቸዋል፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 10:3

በፊትህ

“አንተ እዚያው እያለህ” ይሄ ማለት ካህኑ መለከቱን በሚነፋበት ወቅት ሙሴ እዚያው መገኘት አለበት ማለት ነው፡፡

መሪዎች፤የእሥራኤል ነገድ አለቆች

እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆኑ የነገድ ክፍሎችን የሚያመለክቱ ናቸው፡፡እዚህ ላይ ሁለተኛው ሐረግ ጥቅም ላይ የዋለው የመጀመሪያውን ሐረግ ለማብራራት ሲባል ነው፡፡“የእሥራኤል ነገድ አለቆች የሆኑ መሪዎች”(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

እናንተ ከፍ ባለ ድምፅ መለከት ሰትነፉ

እዚህ ላይ“እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር ነው፡፡እግዚአብሔር ለሙሴ እየተናገረ ቢሆንም የሚያመለክተው ግን ካህናቱን ነው፡፡ካህናቱ እንጂ ሙሴ መለከቱን አይነፋም፡፡“ከፍ ባለ ድምፅ በሚነፉበት ወቅት”(እናንተ የሚለውን በተለያየ መልክ የሚገልፀውንና ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 10:6

እናንተ ከፍ ባለ ድምፅ ስትነፉ

እዚህ ላይ“እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር ነው፡፡እግዚአብሔር ለሙሴ እየተናገረ ቢሆንም የሚያመለክተው ግን ካህናቱን ነው፡፡ካህናቱ እንጂ ሙሴ መለከቱን አይነፋም፡፡“ከፍ ባለ ድምፅ በሚነፉበት ወቅት”(እናንተ የሚለውን በተለያየ መልክ የሚገልፀውንና ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ለሁለተኛ ጊዜ

“ቁጥር 2 ጊዜ”ወይም “እንደገና”(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ማሕበሩ በሚሰባሰብበት ወቅት

“ማሕበሩን በአንድነት መሰብሰብ”

እነርሱ የእነርሱን ጉዞ ለማስጀመር ከፍ ባለ ድምፅ መንፋት ይኖርባቸዋል

“እነርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ካህናቱን ሲሆን “የእነርሱ”የሚለው ቃል ደግሞ የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡

ይሄ ለእናንተ ሥርዓት ይሁን

“ለእናንተ ሕግ ይሁን” እዚህ ላይ “እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር ሲሆን የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡(እናንተ ለሚለው ቃል የተለያዩ አገላለፆች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 10:9

አንተ ወደ ሠልፍ በምትወጣበት..በሚገፏችሁ ወቅት

እግዚአብሔር አንተ የሚለውን ቃል እየተጠቀመ ለሙሴ እየተናገረ ቢሆንም በመሠረቱ የሚናገረው ወደ ጦርነት ለሚወጣው ለእሥራኤል ሕዝብ ነው፡፡“የእሥራኤል ሕዝብ ወደ ጦርነት በሚወጣበት ወቅት…እሥራኤል በምትገፋበት ወቅት”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

ከፍ ባለ ድምፅ መለከቶቹን ይንፉ

እዚሀ ላይ እግዚአብሔር ሙሴን አንተ እያለ እየተናገረው ቢሆንም በመሠረቱ ግን ሙሴ ካህናቱን መለከት እንዲያስነፋቸው ነበር ይናገረው የነበረው፡፡ (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ትታሰባላችሁ

“ትታሰባላችሁ”የሚለው ሐረግ “ትታወሳላችሁ ማለት ነው፡፡“አስባችኋለሁ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 10:10

በዓልን ማክበር

“መከበር”የሚለው ስም “ማክበር”በሚለው ግሥ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በምታከብሩበት ወቅት”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

መለከቱን መንፋት ይኖርባችኋል

እዚህ ላይ እግዚአብሔር ለሙሴ ቢናገርም በመሠረቱ ካህናቱ መለከቱን እንዲነፉ ነው የፈለገው፡፡“ካህናቱ መለከቱን እንዲነፉ ትዕዛዝ መሥጠት ይኖርብሃል”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በወሩ መጀመሪያ

በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት አሥራ ሁለት ወራት አሉ፡፡በብርማ ቀለም የሚደምቀው የጨረቃ በርሃን የመጀመሪያው ምዕራፍ በቀን አቆጣጠሩ ላይ የመጀመሪያው ወር መሆኑን ያመለክታል፡፡(የዕብራውያን ወራት የሚለውን ይመልከቱ)

የሚቃጠል መሥዋዕታችሁ…የደህንነት መሠሥዋዕታችሁ…እናንተ ለእኔ

በእነዚህ ሐረጎች ውስጥ “እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር በመሆኑ የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝበ ነው፡፡(እናንተ ለሚለው ቃል የተለያዩ አገላለፆች የሚለውን መልከቱ)

መሥዋዕታችሁ ላይ

“ለመሥዋዕቱ ከብር”

እነርሱም ለመታሰቢያ ይሆኑላቸኋል

“ለእኔ መታሰቢያ ይሆናችኋል” “መታሰቢያ”የሚለው ቃል “መታሰብ”በሚለው ግሥ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እኔን እንድታሰቡ ያደርጋችኋል”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱም ይሆኑላችኋል

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው መለከቶቹንና መሥዋዕቶቹን ነው፡፡

Numbers 10:11

በሁለተኛውም ዓመት

“2ተኛ ዓመት”ይሄ የሚያመለክተው እግዚአብሔር እሥራኤላውያንን ከግብፅ ያወጣበትን ሁለተኛውን ወር ነው፡፡ (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

በሁለተኛውም ወር ከወሩም በሃያኛው ቀን

“በ2ተኛውም ወር ከወሩም በ20ኛው ቀን”በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት ይሄ ሁለተኛው ወር ነው፡፡”(የዕብራውያን ወራትንና ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ደመናው ተነሳ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ደመናው ብድግ አለ”ወይም “እግዚአብሔር ደመናውን አነሳው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይ መልከቱ)

የመገናኛ ድንኳኑ የምሥክር ሥርዓቶች

መገናኛ ድንኳኑ በዚህ ረዥም በሆነ ሥምም ጭምር የሚጠራበት ምክኒያት የእግዚአብሔር ሕግ ያለበት የቃል ኪዳኑ ሰነድ በውስጡ የሚቀመጥ በመሆኑ ነው፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 1፡50 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በሙሴ በኩል የተሰጠው የእግዚአብሔር ትዕዛዝ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በሙሴ አማካይነት የሰጣቸው ትዕዛዛት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 10:14

በይሁዳ ልጆች ሠፈር ዓርማ ሥር

ይሄ ሠፈር በይሁዳ ሥር የሚገኙ የተለያዩ ነገዶችን የሚያካትት ነው፡፡ይሁዳን፤ይሳኮርንና ዛብሎንን፡፡

በመጀመሪያ ተጓዙ

ሌሎቹ ሁሉ ከሠፈራቸው ከመነሣታቸው በፊት እነርሱ ሠፈራቸውን በመጀመሪያ ለቀው ይሄዱ ነበር፡፡

የአሚናዳብ ልጅ ነአሶን

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የሶገር ልጅ ናትናኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የኬሎን ልጅ ኤልያብ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 10:17

ጌድሶን …ሜራሪ

የእነዚህን ሰዎች ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በሮቤል ሠፈር ዓርማ ሥር የሚገኙ ሠራዊቶች

x

Numbers 10:21

ቀአታውያን

ይሄ የሚያመለክተው የቀአትን የትውልድ ሐረግ ነው፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 3፡27 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በኤፍሬምም ትውልድ ዓርማ ሥር ያሉ ሠራዊቶች

ይሄ የሚያመለክተው በኤፍሬም ክፍል ውስጥ ያሉትን የነገድ ሠራዊቶችን ነው፡፡ሮቤል፤ስምዖንና ጋድ፡፡ኤፍሬም፤ምናሴና ብንያም፡፡

የአሚሁድ ልጅ ኤሊሳማ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡10 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የፍዳሱር ልጅ ገማልኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡10 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የጋዴዮን ልጅ አቢዳን

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 10:25

በዳን ትውልድ ዓርማ ሥር ያሉ ሠራዊቶች

ይሄ የሚያመለክተው በዳን ክፍል ውስጥ ያሉትን የነገድ ሠራዊቶችን ነው፡፡ሮቤል፤ስምዖንና ጋድ፡፡ኤፍሬም፤ምናሴና ብንያም፡፡ዳን፤አሴርና ንፍታሌም፡፡

የአሚሳዳይ ልጅ አኪዔዘር

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡12 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የኤክራን ልጅ ፋግኤል

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የዔናን ልጅ አኪሬ

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 1፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 10:29

የራጉኤል ልጅ ኦባብ

ይሄ የሰው ሥም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር የተናገረውን

“እግዚአብሔር ለእኛ የነገረንን”

መልካም እናደርግልሃለን

“ከመልካም አያያዝ ጋር እንንከባከብሃለን”

Numbers 10:31

ዓይን ትሆንልናለህ

“ዓይን ትሆንልናለህ”ማለት ምሪት መሥጠትና መንከባከብ ማለት ነው፡፡“በበረሃ ውስጥ ምሪት ልትሰጠንና እንዴት መኖር እንደሚገባን ልታሣየን ትችላለህ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 10:33

እነርሱ ተጓዙ

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ተራራ

ይሄ የሚያመለክተው የሲናን ተራራ ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ፍቺ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“የሲና ተራራ፤የእግዚአብሔር ተራራ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔርም የኪዳኑ ታቦት በፊታቸው ይሄድ ነበር

የተወሰኑ ሌዋውያን የቃል ኪዳኑን ታቦት ተሸክመው በእሥራኤል ሕዝብ ፊት ይሄዱ ነበር፡፡“እየተጓዙ እያሉ የተወሰኑ ሰዎች የቃል ኪዳኑን ታቦት ተሸክመው ፊት ለፊት ይሄዱ ነበር”(ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

በቀን ብርሃን

“በየዕለቱ”ወይም “ቀን ሣለ”

Numbers 10:35

ታቦቱ በተጓዘ ዘጊዜ

እዚህ ላይ ታቦቱ ልክ ሰው ይመስል ጉዞ እንደሚጓዝ ዓይነት ነው የሚገለፀው፡፡ታቦቱን የሚሸከሙ ሰዎች ነበሩ፡፡“ታቦቱ በተጓዘ ቁጥር ሰዎች ይሸከሙት ነበር፡፡”(ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

አቤቱ ተነሳ

እዚህ ላይ “ተነሳ”የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር ሥራውን እንዲጀምር የሚጠየቅበት ሲሆን በዚህ አውድ ግን ሙሴ ጠላቶቻቸውን እንዲበትንላቸው እየለመነ ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የሚጠሉህም ከፊትህ ይሸሹ

እዚህ ላይ ሙሴ ጠላቶቹ ከራሱ ከእግዚአብሔር የሚሸሹ ይመስል እግዚአብሔር ጠላቶቻቸውን ከእሥራኤል ሕዝብ እንዲሸሹ ምክኒያት እንዲሆንላቸው ነው የሚለምነው፡፡“አንተን የሚጠሉህን ከታቦትህና ከሕዝብህ እንዲሸሹ አድርጋቸው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ታቦቱ ባረፈ ጊዜ

እዚህ ላይ ታቦቱ ሰው ይመስል እንደሚጓዝ ዓይነት ተደርጎ ነው የሚገለፀው፡፡ታቦቱን የሚሸከሙት ሰዎች ነበሩ፡፡“ሰዎች እንደተሸከሙት ታቦቱ ያርፍ ነበር”(ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

እልፍ አዕላፋት

ይሄ የሚያመለክተው የሰዎቹን ቁጥር ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ትርጉም የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“እልፍ አእላፋት ሕዝብ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 11

1 ህዝቡ ያህዌ እየሰማ ስለ ችግሮቻቸው አጉረመረሙ፡፡ ያህዌ ህዝቡን ሰምቶ ተቆጣ፡፡ ከያህዌ ዘንድ እሳት መጥታ በሰፈሩ ዙሪየ ከነበሩ ሰዎች አንዳንዶችን በላች፡፡ 2 ከዚያም ህዝቡ ወደ ሙሴ ጮኸ፣ ስለዚህም ሙሴ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ እሳቱም ቆመ፡፡ 3 ስፍራው ተቤራ ተብሎ ተጠራ፣ ምክንያቱም የያህዌ እሳት ከመሀላቸው ሰዎችን አቃጥላለች፡፡ 4 አንዳንድ ባዕዳን ከእስራኤላውያን ትውልዶች ጋር መስፈር ጀመሩ፡፡ እነርሱ የተሻለ ምግብ መብላት ፈለጉ፡፡ ከዚያ የእስራኤል ሰዎች ማልቀስና “እንድንበላ ማን ስጋ ሊሰጠን ይችላል” ማለት ጀመሩ፡፡ 5 በግብጽ በነጻ እንበላ የነበረውን አሳውን፣ ዱባውን፣ በጢኹን፣ ባሮ ሽንኩርቱን፣ ቀይ ሽንኩርቱንና ነጭ ሽንኩርቱን እናስታውሳለን፡፡ 6 አሁን ደካሞች ነን፡፡ ከመና በስተቀር ምንም የምንበላው የለም፡፡” 7 መና እንደ ድንብላል ፍሬ ያለ መልክ ነበረው፡፡ ሙጫ ይመስላል፡፡ 8 ሰዎቹ እየተዘዋወሩ ይሰበስቡታል፡፡ በወፍጮ ይፈጩታል፣ በሙጫ ያደቁታል፣ በገንቦዎቹ ይቀቅሉታል፣ ቂጣ አድርገውም ይጋግሩታል፡፡ እንደ ንጹህ የወይራ ዘይት ይጣፍጣል፡፡ 9 ምሽት በሰፈር ውስጥ ጤዛ ሲወርድ፣ መናውም ይወርዳል፡፡ 10 ሙሴ ህዝቡ በየቤቱ ሲያለቅስ አዳመጠ፣ ደግሞም እያንዳንዱ ሰው በእርሱ ድንኳን ደጃፍ ነበር፡፡ ያህዌ በጣም ተቆጥቶ ነበር፣ ደግም የእነርሱ ማጉረምረም በሙሴ እይታ ስህተት ነበር፡፡ 11 ሙሴ ወደ ያህዌ እንዲህ ሲል ጮኸ፣ “ለምን ባሪያህን እንዲህ አስጨነከው? ስለምን በእኔ ደስ አልተሰኘህም? የዚህን ህዝብ ሁሉ ሸክም እንድሸከም አደረግከኝ፡፡ 12 እኔ ይህን ህዝብ ሁሉ ፀንሼዋለሁን? ‘አባት ልጁን እነደሚያቅፍ ይህን ህዝብ ወደ ደረትህ አስጠግተህ ተሸከመው’ ትለኝ ዘንድ እኔ ወልጃቸዋለሁን?’ ትሰጣቸው ዘንድ ለአባቶቻቸው ወደ ማልክላቸው ምድር እንዲገቡ እኔ ልሸከማቸውን? 13 ለእነዚህ ሁሉ ሰዎች የምሰጣቸውን ስጋ ከየት አገኛለሁ? በእኔ ፊት እያለቀሱ እንዲህ ይላሉ ‘የምንበላው ስጋ ስጠን፡፡’ 14 እኔ ብቻዬን ይህን ሁሉ ህዝብ ልሸከም አልችልም፡፡ እጅግ በዝተውብኛል፡፡ 15 እንዲህ እስካደረግኸኝ ድረስ፣ አሁኑኑ ግደለኝ፣ ለእኔ መልካም ከሆንክ፣ መከራዬን ከእኔ አርቅ፡፡” 16 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “ከእስራኤል መሪዎች ሰባዎቹን ወደ እኔ አምጣ፡፡ የህዝቡ መሪዎችና አለቃዎች መሆናቸውን እርግጠኛ ሁን፡፡ ከአንተ ጋር እንዲቆሙ ወደ መገናኛው ድንኳን አምጣው፡፡ 17 እኔ ወርጄ በዚያ ከአንተ ጋር እነጋገራለሁ፡፡ ከአንተ ላይ ካለው መንፈስ ጥቂት ወስጄ በእነርሱ ላይ አደርገዋለሁ፡፡ እነርሱ ከአንተ ጋር የህዝቡን ሸክም ይሸከማሉ፡፡ አንተ ብቻህን ሸክሙን አትሸከምም፡፡ 18 ለህዝቡ እንዲህ በል፣ ‘ነገ ራሳችሁን ለያህዌ ለዩ፡፡ ያህዌ እየሰማ አልቅሳችኋልና፣ በእርግጥ ስጋ ትበላላች፡፡ እንዲህ ብላችኋል፣ “እንበላ ዘንድ ማን ስጋ ይሰጠናል? ለእኛስ በግብጽ መሆን መልካም ነበር፡፡” ስለዚህ ያህዌ ስጋ ይሰጣችኋል፣ እናም ስጋ ትበላላችሁ፡፡ 19 ስጋ የመትበሉት ለአንድ ቀን፣ ለሁለት ቀናት፣ ለአምስት ቀናት፣ ለአስር ቀናት ወይም ለሃያ ቀናት አይደለም፣ 20 ነገር ግን በአፍንጫችሁ እስኪወጣ ድረስ ወር ሙሉ ስጋ ትበላላችሁ፡፡ ነገሩ ያስጸይፋችኋል፣ ምንያቱም በመሀላችሁ ያለውን ያህዌ እምቢ ብላችኋል፡፡ በፊቱ አልቅሳችኋል፡፡ እንዲህ ብላችኋል፣ “ለምን ከግብጽ ወጣን?” 21 ከዚያ ሙሴ እንዲህ አለ፣ “እኔ ከ600000 ሰዎች ጋር ነኝ፣ አንተ ግን እንዲህ አልክ፣ ‘ወር ሙሉ እንዲበሉ ስጋ አበላቸዋለሁ፡፡’ 22 እነርሱን ለማጥገብ እኛ እንስሳትንና የከብት መንጋ ሁሉ እናርዳለን? እነርሱን ለማርካት የባህር አሶችን ሁሉ እናጠምዳን?” 23 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “እጄ አጭር ናትን? አሁን ቃሌ እውነት መሆን አለመሆኑን ታያለህ፡፡” 24 ሙሴ ወጥቶ ለህዝቡ የያህዌን ቃላት ነገራቸው፡፡ ሰባዎቹን የህዝብ መሪዎች ሰበሰበና በድንኳኑ ዙሪያ አቆማቸው፡፡ 25 ያህዌ በደመና ውስጥ ወረዳና ሙሴን ተናገረው፡፡ ያህዌ በሙሴ ላይ ከነበረው መንፈስ ጥቂት ወሰደና በሰባዎቹ ሽማግሌዎች ላይ አደረገው፡፡ መንፈሱ ሲያርፍባቸው፣ ትንቢት ተናገሩ፣ ነገር ግን በዚያ ወቅት እንጂ በሌላ ጊዜ ደግመው አልተነበዩም፡፡ 26 አልዳድና ሞድ የተባሉ ሁለት ሰዎች በሰፈር ቀርተው ነበር፡፡ መንፈሱ በእነርሱ ላይም አረፈ፡፡ ስሞቻቸው በመዝገብ ተጽፎ ነበር፣ ነገር ግን ወደ ድንኳኑ አልሄዱም ነበር፡፡ ሆኖም ግን፣ እነርሱም በሰፈር እያሉ ተነበዩ፡፡ 27 በሰፈር የነበረ አንድ ወጣት ሰው ወደ ሙሴ ሮጦ መጥቶ እንዲህ አለው፣ “ኤልዳድና ሞዳድ በሰፈር ውስጥ እየተነበዩ ነው፡፡” 28 ከእርሱ የተመረጡ ሰዎች አንዱ የሆነው የሙሴ ረዳት የነዌ ልጅ ኢያሱ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “አለቃዬ ሙሴ ሆይ፣ ከልክላቸው፡፡” 29 ሙሴ እያሱን እንዲህ አለው፣ “አንተ ለእኔ ተቆርቁረህ ነውን? እኔ መላው የያህዌ ህዝቦች ነቢያት ቢሆኑ እርሱ በሁሉም ላይ መንፈሱን ቢያደርግ እመኛለሁ!” 30 ከዚያ ሙሴና የእስራኤል ሽማግሌዎች ወደ ሰፈር ተመለሱ፡፡ 31 ከዚያ ከያህዌ ዘንድ ነፋስ ወጥቶ ከባህር ድርጭቶችን አመጣ፡፡ ከሰፈሩ በአንድ በኩል የአንድ ቀን የእግር መንገድ ርቀት ላይ፣ ደግሞም በሌላኛው በኩል በአንድ ቀን የእግር መንገድ ርቀት ድረስ ድርጭቶቹ ወደቁ፡፡ ድርጭቶቹ ሰፈሩን ከመሬት ሁለት ኪዩብ ከፍታ በሚሆን መጠን ሞሉት፡፡ 32 ሰዎቹ ያን ዕለት ምሽቱን ጨምሮ እንዲሁም በማግስቱም ድርጭቶችን በመሰብሰብ ሥራ ተጠምደው ነበር፡፡ ማንም ከአስር የቆሮስ መስፈሪያ ያነሰ ድርጭት አልሰበሰበም፡፡ በሰፈሩ ሁሉ ድርጭቶቹን ተከፋፈሉ፡፡ 33 ስጋው ገና በጥርሳቸው ውስጥ እያላመጡት ሳለ፣ ያህዌ በእነርሱ ላይ ተቆጣ፡፡ ህዝቡን በታላቅ በሽታ መታው፡፡ 34 በዚያ ሥፍራ ስጋ ለማግኘት የጎመጁትን ሰዎች ስለቀበሯቸው የስፍራው ስም ቂብሮት ሃታአባ ተባለ፡፡ 35 ሰዎቹ ከቂብሮት ሃታአባ ወደ ሰፈሩበት ወደ ሐጽሮት ተጓዙ፡፡



Numbers 11:1

የእግዚአብሔርም እሣት በመካከላቸው ነደደች

“እግዚአብሔር የሚያነድን እሣት ላከ”

ለቦታው ሥም ተሰጠው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለዚያ ሥፍራ ሥም ሰጡት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:4

የምንበላውን ሥጋ ማን ይሰጠናል?

እሥራኤላውያን ይህንን ጥያቄ ያቀረቡት ከመና ሌላ ተጨማሪ የሚበሉት ነገር እንደሚፈልጉ ለመጠየቅ ነበር፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሥጋ የመብላት መሻት አለን”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

የምግብ ፍላጎታቸን ጠፋ

“መብላት አንፈልግም” ወይም“” “መብላት አንችልም”

Numbers 11:7

የድንብላል ዘር

የዚህ ዕፅዋት ዘር በሚደርቅበት ጊዜ በቅመምነት ያገለግላል፡፡

ድንብላል

ይሄ የሚያጣብቅ ነገር ያለው ሲሆን የገረጣ ቢጫ ቀለም አለው፡፡

Numbers 11:9

በሙሴ ዓይን

ዓይኑ መመልከቱን የሚያመለክት ሲሆን መመልከቱ ደግሞ አስተሳሰቡን ወይም የፍርድ አሰጣጡን ይወክላል፡፡“በሙሴ አስተሳሰብ”ወይም “በሙሴ ዳኝነት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:11

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ምላሽ የማያሻቸውን ብዙ ጥያቄዎች ለእግዚአብሔር ያቀርባል፡፡(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ለምን በባሪያህ ላይ ክፉ አደረግህ?ለምንስ በፊትህ ሞገስ አላገኘሁም?

ሙሴ እነዚህን ጥያቄዎች የጠየቀው እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ባለው ግንኙነት ላይ የተቃውሞ ጥያቄ ለማቅረብ ነበር፡፡በድርጊት መልክ ሊገለፁ ይችላሉ፡፡ሙሴ ስለራሱ በሶስተኛ አካልነት ነው የሚናገረው፡፡“እኔ ባሪያህን በእንደዚህ ዓይነት መጥፎ ሁኔታ መያዝ አልነበረብህም፡፡በእኔ ልትናደድ አይገባም”ወይም “እኔ ባሪያህ ያጠፋሁት ጥፋት ስለሌለ ጥሩ ባልሆነ ሁኔታ እኔን መያዝ አልነበረብህም!”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄንና የመጀመሪያ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ አካል የሚለውን ይመልከቱ)

የዚህን ሁሉ ሕዝብ ሸክም በእኔ ላይ አደረግህ

ሙሴ ሕዝቡን የመምራቱንና የሚያስፈልጋቸውን ነገር የመሥጠቱን ነገር ልክ ከባድ የሆነ ሸክምን ከመሸከም ጋር ያነፃፅረዋል፡፡“ለእነዚህ ሰዎች ሁሉ ኃላፊነትን ሰጠኸኝ፤እኔ ግን ከብዶኛል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ይህን ሁሉ ሕዝብ እኔ ፀነስኩትን?

ሙሴ ይህን ጥያቄ የሚጠይቀው አባታቸው እንዳልሆነ እግዚአብሔርን ለማሳሰብ ነው፡፡“የእነዚህ ሰዎች ሁሉ አባት አይደለሁም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በብብትህ እቀፋቸው የምትለኝ …ይህን ሕዝብ ወለድኩትን?

ሙሴ እግዚአብሔር እንዲያስታውስለት የፈለገው ምንም እንኳን አባታቸው ባይሆንም እሥራኤላውያንን መንከባከብ እንደሚገባው መናገሩን ነበር፡፡“እኔ ስላልወለድኳቸው እንደ ሕፃን ልጅ ተሸከማቸው ልትለኝ አትችልም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በብብትህ እቀፋቸው

እሥራኤላውያንን መንከባከብ ልክ ዕርዳታ የሚያሻውን ሕፃን ልጅ ከመሸከም ጋር ተነፃፅሯል፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ልሸከማቸው ይገባል …ምን ልስጣቸው?

የዚህ ዓረፍተ ነገር ትርጉም የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“እንድሸከማቸው እንድሰጣቸው መጠበቅ የለብህም!”ወይም “ልሸከማቸው አልችልም...ልሰጣቸው”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:13

ለዚህ ሁሉ ሕዝብ የምሰጠው ሥጋ ከወዴት አገኛለሁ?

ሙሴ ይሄንን ጥያቄ የሚያነሳው ለዚህ ሁሉ ሕዝብ ሥጋ መሥጠት የማይቻል መሆኑን ለመግለፅ ነው፡፡“ለዚህ ሁሉ ሕዝብ የሚበቃ ሥጋ ለማግኘት የምችልበት ሁኔታ የለም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህንን ሕዝብ ለብቻዬ ለመሸከም አልችልም

ሙሴ የመምራቱንና ለሕዝቡ የሚያስፈልጋቸውን ነገር የማቅረቡን ጉዳይ ልክ እነርሱን እንደሚሸከም ዓይነት አድርጎ ይገልፀዋል፡፡“ለእነዚህ ሰዎች ሁሉ የሚያስፈልጋቸውን ነገር ለብቻዬ ለማቅረብ አልችልም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ልሸከማቸው አልችልም

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“ይሄ ኃላፊነት ለእኔ አስቸግሮኛል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:16

በአንተ ካለውም መንፈስ

“መንፈስ”የሚለው ቃል እግዚአብሔር ለሙሴ የተናገረውን ነገር እንዲያደርግ ኃይል የሚሰጠውን የእግዚአብሔርን መንፈስ ነው የሚያመለክተው፡፡“እግዚአብሔር የሰጠህ በአንተ ያለው መንፈስ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የሕዝቡን ሸክም ከአንተ ጋር ይሸከማሉ

እግዚአብሔር የመምራቱንና አስፈላጊ ነገሮችን የማቅረቡን ጉዳይ ልክ ሙሴና ሌሎች መሪዎቹ እንደሚሸከሙት ነገር አድርጎ ነው የሚገልፀው፡፡“የሕዝቡን ሸክም ከአንተ ጋር ይሸከማሉ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ብቻህን መሸከም አይጠበቅብህም

እግዚአብሔር የመምራቱንና ለሕዝቡ አስፈላጊ ነገሮችን የማቅረቡን ጉዳይ ልክ ሙሴና ሌሎች መሪዎቹ እንደሚሸከሙት ነገር አድርጎ ነው የሚገልፀው፡፡“ብቻህን አትሸከማቸውም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:18

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

የምንበላውን ሥጋ ማን ይሰጠናል?

እሥራኤላውያን ይህንን ጥያቄ ያቀረቡት ከመና ሌላ ተጨማሪ የሚበሉት ነገር እንደሚፈልጉ ለመጠየቅ ነበር፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሥጋ የመብላት ፍላጎት አለን”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በአፍንጫችሁ እስኪወጣ

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/እግዚአብሔር ምግቡ በትውከት መልክ በአፍንጫቸው እንደሚወጣ ነው የሚናገረው፡፡“ታምማችሁ እስክታስታውኩ ድረስ”ወይም “በአፍንጫው በሚወጣበት ሁኔታ እጅግ ብዙ ሥጋን ይበላሉ” “በአፍንጫቸው የሚወጣ እስኪመስል ድረስ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ለምን ከግብፅ ወጣን?

ሕዝቡ ይሄንን ጥያቄ የጠየቀው ቅሬታውን ለመግለፅና አቤቱታን ለማቅረብ ነበር፡፡“ከግብፅ ምድር መውጣት አልነበረብንም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:21

600,000 ሕዝብ

“ስድስት መቶ ሺህ ሕዝብ” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

“እነርሱን የሚያጠግብ የበሬና የበግ መንጋ ይታረድን?ወይስ የባህርን ዓሣ ሁሉ ያጠግባቸው ዘንድ ይሰብሰብላቸውን?”

ሙሴ እነዚህን ጥያቄዎች የሚያቀርበው ሕዝቡ እንዲጠግብ ለማድረግ በቂ ሥጋ ስለመኖሩ ጥርጣሬ ስለገባው ነው፡፡ “እነርሱን ለማጥገብ የበሬና የበግ መንጋ እንዲሁም የባህርን ዓሣ ሁሉ መግደል ይኖርብናል”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

መንጎችና ከብቶች

በመሠረቱ እነዚህ ቃላት ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡በአንድነት የሚያመለክቱት ነገር ቢኖር ብዙ ከብቶች የመኖራቸውን ጉዳይ ነው፡፡(ሁለት ተመሳሳይ ገፅታ ያላቸው የሚለውን ይመልክቱ)

የባህርን ዓሣ ሁሉ

“ሁሉ” የሚለው ቃል የተጋነነ ሲሆን ለእሥራኤል ሕዝብ ሁሉ ምግብ ለማቅረብ የማይቻል መሆኑን ለመግለፅ ነው፡፡(የተጋነነ ንፅፅር እና አጠቃላይነት የሚለውን ይመልከቱ)

እንዲጠግቡ ለማድረግ

“ረሃባቸውን ለማስታገስ”

እጄ አጠረችን?

እዚህ ላይ “እጅ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ኃይል ነው፡፡እግዚአብሔር ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው እግዚአብሔር ለሕዝቡ በቂ ሥጋ ሊሰጥ አይችልም ብሎ በማሰቡ ሊገስፀው ነው፡፡“ይህንን የማድረግ በቂ ኃይል የለኝም ብለህ ታስባለህ?”ወይም “ይህንን ለማድረግ ከበቂ በላይ ኃይል እንዳለኝ ማወቅ ይኖርብሃል”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውንና ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:24

የእግዚአብሔር ቃላት

“እግዚአብሔር የተናገረው ነገር”

በሙሴ ላይ ከነበረው መንፈስ

“መንፈስ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ለሙሴ የተሰጠውን የእግዚአብሔርን መንፈስ ነው፡፡ተመሳሳይ ሐረጎችን በኦሪት ዘኁልቁ 11፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ለሙሴ የሰጠው የተወሰነ ኃይል”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በሰባዎቹ ሽማግሌዎች ላይ አድርግ

ለሽማግሌዎቹ ኃይልን መሥጠት መንፈስን በእነርሱ ላይ ማድረግ በሚል መልኩ ነው የተገለፀው፡፡ተመሣሣዩን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 11፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ለሰባ ሽማግሌዎች ሰጠ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

መንፈሱም በላያቸው ላይ ባደረ ጊዜ

ከመንፈሱ ኃይል ማግኘትን መንፈሱ እንደወረደባቸው ተደርጎ ተነግሯል፡፡“ከመንፈሱ ኃይልን ባገኙበት ወቅት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:26

መንፈሱም በላያቸው አደረ

ከመንፈሱ ኃይል ማግኘትን መንፈሱ እንደወረደባቸው ተደርጎ ተነግሯል፡፡“መንፈሱ ኃይልን ሰጣቸው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ስማቸው በዝርዝሩ ውስጥ ተፅፎ ነበረ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴ ሥማቸውን በዝርዝሩ ውስጥ ፃፈው”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:28

ከልክላቸው

“መተንበዩን እንዲያቆሙ ንገራቸው”

ስለ እኔ አንተ ትቀናለህን?

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የጠየቀው እግዚአብሔርን ለመውቀስ ነበር፡፡አስፈላፊ ሆኖ ከተገኘ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለእኔ ስትል ልትቀና አይገባህም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ስለ እኔ አንተ ትቀናለህን?

አስፈላጊ ከሆነ እግዚአብሔር የሚቀናበት ነገር ምን እንደሆነ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ለእኔ የሆነውን ነገር ሊወስዱ ይችላሉ ብለህ ሰጋህን?”ወይም “ሰዎች ሥልጣኑን አያከብሩለትም ብለህ ተጨነቅክን?”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

መንፈሱን በእነርሱ ላይ ያደርግ ዘንድ

ሙሴ ለሰዎች ኃይል የሚሰጠውን የእግዘአብሔርን መንፈስ ልክ እግዚአብሔር መንፈሱን በእነርሱ ላይ እንደሚያስቀምጥ አድርጎ ይገልፀዋል፡፡“የእግዚአብሔር መንፈስ ኃይልን ሁሉ ይሰጣቸው ዘንድ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:31

ድርጭት

“ትንሽ ወፍ”(ያልታወቁትን መተርጎም የሚለውን ይመልከቱ)

የአንድ ቀንም መንገድ ያህል በዚህ የአንድ ቀንም ያህል መንገድ በዚያ

“በእያንዳንዱ አቅጣጫ አንድ ሰው ቀኑን ሙሉ የሚጓዝበትን መንገድ ያህል”

ሁለት ክንድ ያህል

ክንድ የመለኪያ ዓይነት ሲሆን 46 ሴንቲ ሜትር አካባቢ ይሆናል፡፡“92 ሴንቲ ሜትር ያህል” ወይም “አንድ ሜትር ያህል” (መፅሐፍ ቅዱሣዊ ርቀትንና ቁጥሮችን ይመልከቱ)

ከአሥር የቆሮስ መስፈሪያ በታች የሰበሰበ አልነበረም

ይሄ ድርብ አሉታዊ ሲሆን በአዎንታዊ ዓረፍተ ነገር ሊገለፅም ይችላል፡፡

አሥር የቆሮስ መስፈሪያ

የቆሮስ መሥፈሪያ የመለኪያ ዓይነት ሲሆን 220 ሊትር ያህል ይሆናል፡፡“220 ሊትር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ የመጠን መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 11:33

ሥጋውም ገና በጥርሳቸው መካከል ሳለ ሳያኝኩትም

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡አንድ ላይ በመሆን አፅንዖት የሚሰጡት ሥጋውን ገና እየበሉ እያሉ ያኔውኑ እግዚአብሔር ቅጣቱን የላከባቸው መሆኑን ነው፡፡“ገና ሥጋውን እየበሉ እያሉ”(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የዚያ ሥፍራ ሥም የምኞት መቃብር ተብሎ ተጠራ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሥፍራውን የምኞት መቃብር ብለው ጠሩት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውንና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ሐፂሮት

ይሄ በበረሃ ውስጥ የሚገኝ የአንድ ስፍራ ስም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 12

1 “ከዚያ ማርያም እና አሮን ሙሴ ባገባት ኩሻዊ ሴት ምክንያት በሙሴ ላይ በተቃውሞ ተናገሩ፡፡ 2 እንዲህም አሉ፣ “ያህዌ የተናገረው ከሙሴ ጋር ብቻ ነውን? ከእኛስ ጋር አልተናገረምን?” ያህዌ እነርሱ የተናገሩትን ሰማ፡፡ 3 ሙሴ ፣ በምድር ላይ ከሚገኝ ከማንኛውም ሰው ይልቅ በጣም ትሁት ሰው ነበር፡፡ 4 ወዲያውኑ ያህዌ ከሙሴ፣ ከአሮንና ማርያም ጋር ተናገረ “እናንተ ሶስታችሁ ወደ መገናኛው ድንኳን ውጡና ኑ፡፡” ስለዚህም ሶስቱም ወጥተው መጡ፡፡ 5 ከዚያም ያህዌ በደመና አምድ ወረደ፡፡ በድንኳኑ መግቢያ ቆሞ አሮንንና ማርያምን ጠራቸው፡፡ ሁለቱም ወደ ፊት ቀረቡ፡፡ 6 ያህዌ እንዲህ አለ፣ “አሁን ቃሎቼን ስሙ፡፡ አንድ የእኔ ነብይ በመካከላችሁ ሲሆን፣ ራሴን፣ በራዕይ እገልጥለታለሁ፣ በህልምም እናገረዋለሁ፡፡ 7 አገልጋዬ ሙሴ ግን እንደዚያ አይደለም፡፡ እርሱ በቤቴ ላይ ሁሉ የታመነ ነው፡፡ 8 እኔ ከመሴ ጋር በቀጥታ እናገራሁ፣ በራዕይ ወይም በዘይቤ አይደለም፡፡ እርሱ የእኔን መልክ ያያል፡፡ ስለዚህ በአገልጋዬ በሙሴ ላይ ስትናገሩ ለምን አልፈራችሁም?” 9 የያህዌ ቁጣ በእነርሱ ላይ ነደደ፣ ከዚያም ትቷቸው ሄደ፡፡ 10 ደመናው ከድንኳኑ ላይ ተነሳ፣ እናም ማርያም በድንገት በለምጽ ተመታች እንደ በረዶ ነጭ ሆነች፡፡ አሮን ወደ ማርያም ዞር ብሎ ሲመለከታት በልምጽ መመታቷን አየ፡፡ 11 አሮን ሙሴን እንዲህ አለው፣ “ጌታዬ ሆይ፣ እባክህን በአንተ ላይ የፈጸምነውን ይህን በደል አትቁጠርብን፡፡ በስንፍና ተናግረናል፣ ደግሞም በድለናል፡፡ 12 እባክህን ከእናቱ ማህጸን ሲወጣ ጭንጋፍ ሆኖ እንደ ተወለደ ከፊል አካሉ እንደተበላ ሆና አትተዋት፡፡” 13 ስለዚህም ሙሴ ወደ ያህዌ ጮኸ፡፡ እንዲህም አለ፣ “እግዚአብሔር ሆይ፣ እባክህ፣ እባክህ ፈውሳት፡፡” 14 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “አባቷ በፊቷ ላይ ቢተፋባት፣ ለሰባት ቀናት በሀፍረት ትቆያለች፡፡ ከሰፈር ውጭ ለሰባት ቀናት ዝጋባት፡፡ ከዚያ በኋላ መልሰህ አምጣት፡፡” 15 ስለዚህም ማርያም ከሰፈር ውጭ ለሰባት ቀናት ተዘጋባት፡፡ እርሷ ወደ ሰፈር እስክትመለስ ድረስ ህዝቡ ጉዞ አላደረገም፡፡ 16 ከዚያ በኋላ፣ ህዝቡ ከሐዴሮት ተነስቶ ተጓዘና በፋራን ምድረበዳ ሰፈረ፡፡



Numbers 12:1

በውኑ እግዚአብሔር በሙሴ ብቻ ተናግሯልን?በእኛሰ ደግሞ የተናገረ አይደለምን?

ማርያምና ሙሴ ይሄንን ጥያቄ የጠየቁት ሙሴ ብዙ ሥልጣን ሲኖረው እኛ ግን የሚገባንን ያህል ሥልጣን የለንም በሚል ምክኒያት ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር የተናገረው ለሙሴ ብቻ አይደለም፡፡ከእኛም ጋር ተነጋግሯል፡፡”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

አሁን እግዚአብሔር ሰማ

እዚህ ላይ “አሁን”የሚለው ቃል ከዚህ ቀጥሎ ላለው አስፈላጊ ነጥብ ሰው የበለትኩረት እንዲሰጥ ያደርጋል፡፡

አሁን ሰው የሆነው ሙሴ

“አሁን”የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው በዋናው ታሪክ ላይ እረፍት ለመሥጠት ነው፡፡ተራኪው የሙሴን ባህርይ በሚመለከት የጀርባ ታሪኩን ይናገራል፡፡(የጀርባ ታሪክ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 12:4

የደመና አምድ

የደመናው ቅርፅ አምድ እንደሆነ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“የአምድ ቅርፅ ያለው ደመና”ወይም “ረዥም ደመና” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 12:6

ባሪያዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም

“ለሙሴ እንደዚያ አልናገርም”

በቤቴ ሁሉ የታመነ ነው

እዚህ ላይ ቤቴ የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን አገር ነው፡፡በእግዚአብሔር ቤት ታማኝ መሆን እሥራኤልን ለመምራት ታማኝ መሆንን ያመለክታል፡፡“ሙሴ ሕዝቤን በታማኝነት ይመራል”ወይም“ሕዝቤን እሥራኤልን እንዲመራ እምነት የምጥልበት ሙሴን ነው” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በባሪዬ በሙሴ ላይ ትናገሩ ዘንድ ስለምን አልፈራችሁም?

እግዚአብሔር ይህንን ጥያቄ የጠየቀው ማርያምንና አሮንን ለመገሰፅ ነው፡፡በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይቸላል፡፡“ባሪያዬን ሙሴን በመቃወም ለመናገር መፍራት ነበረባችሁ፡፡”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በባሪያዬ ላይ፤በሙሴ ላይ

“በሙሴ ላይ”የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር የሚናገረው ባሪያው እርሱ ስለመሆኑ ግልፅ ይሆናል፡፡“በባሪያዬ በሙሴ ላይ”(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 12:9

የእግዚአብሔርመ ቁጣ በእነርሱ ላይ ነደደ

የእግዚአብሔር ቁጣ እሣት እንደሆነ ዓይነት ተደርጎ ነው የተነገረው፡፡“እግዚአብሔር በእነርሱ ላይ በጣም ተቆጣ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ በረዶ ነጭ ሆነ

ለምፅ የማርያምን ሥጋ ወደ ነጭነት ቀየረው፡፡“በጣም ነጭ ሆነ”(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 12:11

እባክህ ኃጢአታችንን አትያዝብን

የሰዎችን ኃጢአት መያዝ ማለት ለፈፀሙት ኃጢአት ተጠያቂ ናቸው ማለት ነው፡፡ይሄ የሚያመለክተው በኃጢአታቸው የመቀጣታቸውን ጉዳይ ነው፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ከእናቱ ሆድ በወጣ ጊዜ ግማሽ ሥጋው ተበልቶ እንደሞተ አትሁን

በማርያም ላይ የተጣበቀባት ለምፅ ሕይወቷ እስኪያልፍ ድረስ ሥጋዋ እየበሰበሰ እንዲሄድ የሚያደርግ ነበር፡፡እየበሰበሰ የሚሄደው ሥጋ ልክ እንደሚባላ ነገር ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ከእናቱ ሆድ በወጣ ጊዜ ግማሽ ሥጋው ተበልቶ እንደሞተ አትሁን”(ተነፃፃሪ የሚለውንና ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 12:13

እባክህ ፈውሳት፤እባክህ አግዚአብሔር

“እባክህ”የሚለው ቃል የተደገመው ለጉዳዩ አፅንዖት ለመሥጠት ነው፡፡

አባትዋ ምራቁን በላይዋ ላይ ቢፋባት

ይሄ የሚያመለክተው ሊሆን ይችል የነበረ ነገር ተግባራዊ አለመደረጉን ነው፡፡በአንድ ሰው ፊት ላይ ምራቅ መትፋት ትልቅ ስድብ ነበር፡፡(በግምት ላይ የተመሠረቱ ሁኔታዎችንና ተምሣሌታዊ ድርጊቶች የሚለውን ይመልከቱ)

ማርያምም ከሠፈር ውጪ ተዘግታ ተቀመጠች

ከሠፈር ውስጥ ከወጣች በኋላ ተመልሣ ለመምጣት ያለመቻሏን ሁኔታ ልክ ከጀርባዋ በር እንደተቆለፈባት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ማርያም ከሠፈር ውጪ እንደትሄድ ተደረገ”ወይም “ማርያም ከሠፈር ውጪ እንድትሆን ተደረገ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ማርያም ከሠፈር ውጪ ነበረች

ይሄ በድርጊት መልከ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴ ማርያምን ከሠፈር ውጪ ዘጋባት”ወይም “ሙሴ ማርያምን ከሠፈር ውጪ ላካት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 12:16

ሐጺሮት

ይሄ በበረሃ ውስጥ ያለ የአንድ ሥፍራ ሥም ነው፡፡ይህንን በኦሪት ዘኁልቁ 11፡35 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡


Chapter 13

1 ዚያም ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 ”ለእስራኤላውያን የሰጠኋቸውን የከነዐንን ምድር እንዲያዩ ጥቂት ሰዎችን ላክ፡፡ ከአባቶቻቸው ከእያንዳንዱ ነገድ አንድ ሰው ላክ፡፡ ከመሀላቸው የሚላከው እያንዳንዱ ሰው መሪ መሆን አለበት፡፡” 3 ሙሴ የያህዌን ትእዛዝ እንዲያደርጉ ከፋራን ምድረ በዳ ላካቸው፡፡ ሁሉም ከእስራኤል ሰዎች መሃል የተመረጡ መሪዎች ነበሩ፡፡ 4 ስሞቻቸው እነዚህ ነበሩ፡ ከሮቤል ነገድ፣ የዘኩር ልጅ ሳሙኤል፡፡ 5 ከስምዖን ነገድ፣ የሱሬ ልጅ ሰፈጥ፡፡ 6 ከይሁዳ ነገድ፣ የዩፎኒ ልጅ ካልብ፡፡ 7 ከይሳኮር ነገድድ የዮሴፍ ልጅ ይግአል፡፡ 8 ከኤፍሬም ነገድ፣ የነዌ ልጅ አውሴ፡፡ 9 ከብንያም ነገድ፣ የራፋ ልጅ ፈልጢ፡፡ 10 ከዛብን ነገድ፣ የሰዲ ልጅ ጉዲኤል፡፡ 11 ከዮፍ ትውልዶች፣ ይህም፣ ከምናሴ ነገድ ነው፣ የሱሲን ልጅ ጋዲ፡፡ 12 ከዳን ነገድ፣ የገማሊ ልጅ ዓሚኤል፡፡ 13 ከአሴር ነገድ፣ የሚካኤል ልጅ ሰቱር፡፡ 14 ከንፍታሌም ነገድ፣ የያቢ ልጅ ናቢ፡፡ 15 ከጋድ ነገድ፣ የማኪ ልጅ ጉዲኤል ነበሩ፡፡ 16 ምድሪቱን እንዲያዩ ሙሴ የላቸው ሰዎች ስሞች እነዚህ ነበሩ፡፡ ሙሴ የነዌ ልጅ አውሴን፣ ኢያሱ ብሎ ጠራው፡፡ 17 ሙሴ እነርሱ የከነዓንን ምድር እንዲያዩ ላካቸው፡፡ እንዲህ አላቸው፣ “ከነጌብ ጀምራችሁ እስከ ተራራማው አገር ድረስ ሂዱ፡፡ 18 ምድሪቱ ምን እንደምትመስል ተመልከቱ፡፡ በዚያ የሚኖሩ ሰዎችን እዩ፣ ጠንካሮች ወይም ደካሞች መሆናቸውን፣ እና ጥቂት ወይም ብዙ መሆናቸውን ተመልከቱ፡፡ 19 የሚኖሩባት ምድር ምን እንደምትመስል እዩ፡፡ መልካም ናት ወይስ መጥፎ? በዚያ ምን አይነት ከተሞች አሉ? ሰፈር አይነት ናቸው? የተቀጠሩ ከተሞችስ ናቸውን? 20 ምድሪቱ ምን እንደምትመስል እዩ፣ ለእርሻ የተመቸች ናት ወይስ አይደለችም፣ በዚያ ዛፎች አሉ ወይስ የሉም፡፡ ብርቱ ሁኑና ከምድሪቱ ምርት ከየአይነቱ ይዛችሁ ኑ፡፡” ወቅቱ የወይን ፍሬ ማፍራት የጀመረበት ነበር፡፡ 21 ስለዚህ ሰዎቹ ወጥተው በሌለቦ ሐማት አጠገብ፣ ከጺን ምድረበዳ እስከ ሌቦ ድረስ ምድሪቱን ተመለከቱ፡፡ 22 ከኔጌብ ወጥተው እስከ ኬብሮን ደረሱ፡፡ ከዔናቅ ነገድ ዝርያ የሆኑ የአኪመን፣ የሴሲና፣ እና የተላሚ ነገዶች በዚያ ነበሩ፡፡ ኬብሮን ግብጽ ውስጥ የተመሰተረችው ከከጣኔዎስ ሰባት አመት ቀደም ብላ ነበር፡፡ 23 ኤሽኮል ሸለቆ ሲደርሱ፣ የወይን ዘለላ የያዘ ቅርንጫፍ ቆረጡ፡፡ ከቡድናቸው በሁለቱ መሃል በበትር አድርገው የወይኑን ዘለላ ተሸከሙት፡፡ እንደዚሁም ሮማንና በለስም አመጡ፡፡ 24 የእስራኤል ሰዎች በዚየ ከቆረጡት የወይን ዘለላ የተነሳ፣ ያቺ ስፍራ የኤሽኮል ሸለቆ ተብላ ተጠራች፡፡ 25 ምድሪቱን መርምረው ከአርባ ቀናት በኋላ ተመለሱ፡፡ 26 የተላኩት ሰዎች፣ ሙሴና አሮን እንዲሁም መላው የእስራኤል ማህበረሰብ ወዳሉበት በፋራን ምድረበዳ ወደምትገኘው ወደ ቃዴስ መጡ፡፡ ወደ እነርሱና ወደ መላው ማህበረሰብ ተመልሰው መጥተው፣ የምድሪቱን ፍሬ አሳይዋቸው፡፡ 27 ሙሴን እንዲህ አሉት፣ “ወደ ላከን ምድር ደረስን፡፡ በእርግጥም ወተትና ማር ታፈሳለች፡፡ ከምድሪቱ ምርት እነሆ፡፡ 28 ሆኖም፣ በዚያ የሚኖሩ ሰዎች ብርቱዎች ናቸው፤¨ከተሞቹም የተመሸጉና ትላልቅ ናቸው፡፡ ደግሞም በዚያ የዔናቅን ዝርያዎችም አይተናል፡፡ 29 አማሌቃውያን በነጌብ ይኖራሉ፡፡ ኬጢያውያን፣ ኢያቡሳዊያን፣ እና አሞራዊያን በተራራማው አገር ይኖራሉ፡፡ ከነዓናዊያን በባህሩ አቅራቢያ በዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ ይኖራሉ፡፡” 30 ከዚያ ካሌብ በሙሴ ዙሪያ የተሰበሰቡበትን ሰዎች ሊያበረታታቸው ተነሳ፣ እንዲህም አለ፣ “በአንድ ጊዜ ተነስተን እንውጣና ምድራቸውን እንውረስ፣ ምክንያቱም በሚገባ ልናሸንፍ እንችላለን፡፡” 31 ግን ከእርሱ ጋር የሄዱት ሌሎች ሰዎች እንዲህ አሉ፣ “እኛ ሰዎቹን ማጥቃት አንችልም ምክንያቱም እነርሱ ከእኛ ይልቅ ጠንካሮች ናቸው፡፡” 32 ስለዚህም ስለተመለከቷት ምድር በእስራኤለ ሰዎች መሀል ተስፋ አስቆራጭ ወሬ አሰራጩ፡፡ እንዲህም አሉ፣ “የተመለከትናት ምድር በላይዋ የሚኖሩትን የምትበላ ናት፡፡ በዚያ ያየናቸው ሰዎ ሁሉ ቁመተ ረጃጅም ሰዎች ናቸው፡፡ 33 በዚያ የኤናቅ ዝርያዎችን አይተናል፣ ከግዙፋኑ ሰዎች የመጡትን ግዙፎቹን ሰዎች አይተናል፡፡ ከእነርሱ ጋር ስንተያይ፣ በእኛ በራሳችን ዐይን እንደ አንበጣ ነበርን፣ ደግሞም በእነርሱም ዐይን እንደዚሁ ነበርን፡፡”



Numbers 13:1

የምሰጣትን

እግዚአብሔር የከነዓንን ምድር ለእሥራኤል ሕዝብ ለመስጠት የወሰነ ቢሆንም ወደዚያ ግን አልገቡም ነበር፡፡“ልሰጥ የወሰንኩትን”ወይም “በቅርቡ የምሰጠውን”(የቆየ ትንቢት የሚለውን ይመልከቱ)

እያንዳንዱ በመካከላቸው አለቃ ይሁን

“አንተ የላክኸው እያንዳንዱ ሰው በነራሱ ነገድ መካከል አለቃ መሆን ይኖርበታል፡፡”

Numbers 13:3

የዘኩር ልጅ ሰሙኤል

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 13:5

ሰፈጥ…ኡሪ…ዮፎኒ…ይግአል…ዮሴፍ..ነዌ

እነዚህ ሁሉ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 13:9

ፈልጢ…ራፉ…ጉድኤል…ጋዲ…ሱሲ…አሚኤል…ገማሊ

እነዚህ ሁሉ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ከዮሴፍ ነገድ አርሱም የምናሴ ነገድ

በዮሴፍና በምናሴ መካከል ያለው ግንኙነት የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ከዮሴፍ ልጅ ከምናሴ ነገድ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 13:13

ሰቱር…ሚካኤል…ናቢ ያቢ…ጉዲኤል…ማኪ

እነዚህ ሁሉ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የነዌ ልጅ አውሴ

የእነዚህን ሰዎች ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 13፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 13:17

ምድሪቱ መልካም ወይም ክፉ፤የሚኖሩባቸው ከተሞች ሠፈሮች ወይም አምባዎች እንደሆኑ እዩ

ሙሴ ይህን ጥያቄ የሚጠይቀው የተላኩት ሰዎች በሚመለሱበት ወቅት ሊያቀርቡ የሚገባቸውን መረጃ በሚመለከት ግልፅ ለማድረግ በመፈለግ ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ “ምድሪቱ መልካም ወይም ክፉ፤ምን ዓይነት ከተሞች እንዳሉ፤ከተሞቹ ሰዎች የሚኖሩባቸው ሠፈሮች ብቻ እንደሆኑ ወይም የጦር ምሽግ መኖር አለመኖሩን አጣሩ” (ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ ሠፈሮች ናቸው ወይስ የተመሸጉ ከተማዎች ናቸው?

የተመሸጉ ከተሞች ራሣቸውን ከጠላት ጦር ለመከላከል ሲሉ ጠንካራ ቅጥሮች ይኖሯቸዋል፡፡ሠፈሮች ግን እንደዚህ ዓይነት ቅጥሮች የሏቸውም፡፡

Numbers 13:21

ጺን…ሐማት..ረአብ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የጺን ምድረ በዳ

እዚህ ላይ “ጺን” የሚለው ቃል በዕብራይስጥ ቋንቋ ምድረ በዳ ማለት ነው፡፡(ቃላትን መዋስና መቅዳት የሚለውን ይመልከቱ)

ኬብሮንም በግብፅ ካለችው ከጣኔዎስ በፊት ሰባት ዓመት ተሠርታ ነበር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ግብፃውያን ጺንን ከመገንባታቸው ሰባት ዓመታት በፊት ከነዓናውን ኬብሮንን ገንብተዋት ነበር” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

አኪመን…ሴሲ…ተላሚ

እነዚህ በየአባቶቻቸው ቤቶች የነገድ ስሞች አንፃር የተሰየሙ ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ዔናቅ

ይሄ የሰው ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 13:23

ኤሽኮል

ይሄ የቦታ ስም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

በሁለቱ ወገኖቻቸው መካከል

“በየወገኖቻቸው ባሉ ሁለት ሰዎች መካከል”

የዚያን ሥፍራ ሥም …ብለው ጠሩት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለዚያ ሥፍራ ሥም ሰጡት” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 13:25

ከአርባ ቀናት በኋላ

“ከ40 ቀናት በኋላ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ቃል ይዘው ተመለሱ

“ቃል”የሚለው የሚያመለክተው መረጃን ነው፡፡“መረጃቸውን ይዘው ተመለሱ” ወይም “የተመለከቱትን ነገር ዘገቡ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 13:27

እርስዋም ወተትና ማር ታፈስሳለች

“በእርግጥም ወተትና ማር እዚያ ይፈስሳሉ”ምድሪቱ ለእንስሳትና ለዕፅዋት ተስማሚ መሆኗን ለመግለፅ ከእነዚያ እንስሳት የሚገኘው ወተትና ማር በምድሪቱ ላይ እንደሚፈስስ ነገር አድርገው ይገልፁታል፡፡“ከብቶችን ለማሳደግና አህልን ለማግኘት ድንቅ የሆነ ሥፍራ ነው”ወይም “በእርግጥም ለምለም የሆነ አገር ነው”ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ወተት

ወተት ከላምና ከፍየል የሚገኝ ነገር በመሆኑ ከብቶችንና ከከብቶች የሚገኘውን ምገብ ያመለክታል፡፡“ከከብቶች የሚገኝ ምግብ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ማር

ማር ከአበቦች የሚገኝ ነገር በመሆኑ ዕፅዋትንና ከዕፅዋት የሚገኘውን ምገብ ያመለክታል፡፡“ከዕፅዋት የሚገኝ ምግብ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 13:32

እነርሱ ስለ ሰለልዋትም … እያወሩ

እዚህ ላይ “እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ከካሌብና ከኢያሱ በስተቀር በጊዜው ለስለላ የሄዱትን ሰዎች ሁሉ ነው፡፡

የሚኖሩባትን ምድር የምትበላ ምድር

ሰዎቹ ምድሪቱ ወይም በምድሪቱ የሚኖሩ ሰዎች እጅግ አደገኞች መሆናቸውን ለመግለፅ ምድሪቱ ሰዎችን የምትበላ እንደሆነች አድርገው ያቀርቡታል፡፡“እጅግ አደገኛ ምድር”ወይም “ሰዎቹ ነፍሳችንን የሚያጠፉበት ምድር” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ዔናቅ

ይሄ የሰው ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

እኛ በዓይናችን ግምት …እኛ በዓይናቸው ዘንድ

እዚህ ላይ “ማየት” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ግምገማንና የፍርድ ውሳኔ መሥጠትን ነው፡፡“በእኛ አስተሳሰብ…በእነርሱ አስተሳሰብ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በዓይናችን ግምት እንደ አንበጣ ነበርን

ሰዎቹ ስለ አንበጣ የተናገሩት በዚያ ምድር ካሉት ሰዎች ጋር ራሣቸውን ሲያነፃፅሩ ምን ያሀል ትንሽ መሆናቸው እንደተሰማቸው ለመግለፅ ብለው ነው፡፡“እኛን ከእነርሱ ጋር ስናነፃፅረው የአንበጣ ያህል ትናንሾች ነን›፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 14

1 “በዚያን ምሽት ማህበረሰቡ በሙሉ ድምጹን ከፍ አድርጎ አለቀሰ፡፡ 2 እስራኤል ሰዎች ሁሉ ሙሴንና አሮንን ነቀፉ፡፡ መላው ማህበረሰብ እንዲህ አሏቸው፣ “በግብጽ ምድር ብንሞት ይሻለን ነበር፡፡ ውይም ምነው በዚህ በረሃ በሞትን ኖሮ! 3 ያህዌ ለምን በዚህ ምድረበዳ በሰይፍ እንድንሞት ወደዚህ ምድር አመጣን? ሚስቶቻችንና ትናንሽ ልጆቻችን የተጠቁ ይሆናሉ፡፡ ወደ ግብጽ መመለስ አይሻለንምን?” 4 እርስ በእርሳቸው እንዲህ ተባባሉ፣ “ሌላ መሪ እንምረጥ፣ እናም ወደ ግብጽ እንመለስ፡፡” 5 ከዚያ ሙሴና አሮን በእስራኤል ህዝብ በማህበረሰቡ ጉባኤ ፊት በግምባራቸው ተደፉ፡፡ 6 ምድሪቱን ለማየት ከወጡት ውስጥ ከነበሩት የነዌ ልጅ ኢያሱና የዩፎኒ ልጅ ካሌብ ልብሳቸውን ቀደዱ፡፡ 7 እስራኤል ሰዎች መላው ማህበረሰብ እንዲህ ሲሉ ተናገሩ፣ “በውስጧ ያለፍነውና የተመለከትናት ምድር በጣም መልካም መድር ናት፡፡ 8 ያህዌ በእኛ ደስ ከተሰኘ፣ ወደዚህች ምድር ያስገባናል ደግሞም እርሷን ለእኛ ይሰጠናል፡፡ ምድሪቱ ወተትና ማር የምታፈስ ናት፡፡ 9 ነገር ግን በያህዌ ላይ አታምጹ፣ ደግሞም በምድሪቱ የሚኖሩትን ህዝቦች አትፍሩ፡፡ በቀላሉ እንደ ምግብ እንበላቸዋለን፡፡ ጥላቸው ከእነርሱ ተገፏል፣ ምንያቱም ያህዌ ከእኛ ጋር ነው፡፡ እነርሱን አትፍሯቸው”፡፡ 10 ነገር ግን መላው ማህበረሰብ እስከ ሞት ሊወግሯቸው ተነሰቡቸው፡፡ ከዚያ የያህዌ ክብር በመገናኛው ድንኳን ለመላው የእስራኤል ሰዎች ታየ፡፡ 11 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “ይህ ህዝብ እስከ መቼ እኔን ይንቀኛል በመካከላቸው በሃይሌ ያደረኳቸውን ምልክቶች እያዩ እንኳን እስከ መቼ በእኔ አያምኑም 12 በበሽታ እመታቸዋለሁ፣ ወደ ርስታቸው አላስገባቸውም፣ ሆኖም ከአንተ ከራስህ ነገድ ከእነርሱ ይልቅ ታላቅና ሃያል ህዝብ አበጃለሁ፡፡” 13 ሙሴ ያህዌን እንዲህ አለው፣ “ይህን ብታደርግ፣ ግብጻዊያን ስለዚህ ነገር ይሰማሉ፣ ምክንያቱም አንተ ይህን ህዝብ በኃይልህ ከእነርሱ አድነሃቸዋል፡፡ 14 ለዚህች ምድር ነዋሪዎች ይህንን ይናገራሉ፡፡ አንተ ያህዌ፣ ከዚህ ህዝብ ጋር እንደሆንክ እነርሱ ሰምተዋል፣ ምክንያቱም አንተ ፊት ለፊት ታይተሃል፡፡ የአንተ ደመና በእኛ ህዝብ ላይ ሆኗል፡፡ አንተ በእነርሱ ፊት በቀን በደመና አምድ በምሽት በእሳት አምድ ሄደሃል፡፡ 15 አሁን ይህንን ህዝብ እንደ አንድ ሰው ብትገድል፣ ዝናህን የሰሙ ህዝቦች እንዲህ ይላሉ፣ 16 ‘ያህዌ ይህንን ህዝብ ሊሰጣቸው ወደ ማለላቸው ምድር ሊያስገባቸው ባለመቻሉ ምክንያት፣ በምድረበዳ ገደላቸው፡፡ 17 አሁን፣ እኔ እለምንሃለሁ፣ ታላቁን ሀይልህን ተጠቀም፡፡ አንተ እንዲህ ብለሃልና፣ 18 ‘ያህዌ ለቁጣ የዘገየ ነው፣ በቃል ኪዳን ታማኝነቱ የተትረፈረፈ ነው፡፡ እርሱ በደልና መተላለፍን ይቅር ይላል፡፡ የአባቶችን ኃጢአት ቅጣት እስከ ሁለትና ሶስት ትውልድ በልጆቻቸው ላይ ሲያመጣ በደላቸውን በምንም አይነት ሳይቀጣ አይቀርም፡፡’ 19 የቃል ኪዳን ታማኝነነትህን ታላቅነት ስላልተረዳ ይህ ህዝብ ይበድላል፣ በግብጽ ከነበሩበት ጊዜ አንስቶ እስከ አሁን ሁልጊዜም ይቅር እንዳልካቸው ይቅር እንድትል እለምንሃለሁ፡፡” 20 ያህዌ እንዲህ አለው፣ “ልመናህን ሰምቼ ይቅር ብያቸዋለሁ፣ 21 ነገር ግን፣ እኔ ሕያው ስለሆንኩና መላው ምድርም በእኔ ክብር የተሞላች ስለሆነች፣ 22 ክብሬን፣ በግብጽና በምድረበዳው ጉዟቸው ያደረኳቸውን የሀይሌን ምልክቶች አይተው እነዚያ ህዝቦች ሁሉ - እስከ አሁን ድረስ በእነዚህ አስር ጊዜ ተፈታተኑኝ እንጂ ድምጼን አልሰሙም፡፡ 23 ስለዚህ ለአባቶቻቸው የማልኩላቸውን ምድር በፍጹም አያዩም፡፡ እኔን ከናቁት ውስጥ አንዳቸውም ምድሪቱን አያዩም፣ 24 ከባሪያዬ ከካሌብ በስተቀር፣ ምክንያቱም እርሱ የተለየ መንፈስ አለው፡፡ እርሱ እኔን በሙሉ ልቡ ተከትሎኛል፣ ሊያያት ወደሄደበት ምድር እኔ እመጣዋለሁ፡፡ የእርሱ ትውልዶች ይወርሷታል፡፡ 25 (አሁን አማሌቃዊያንና ከነዓናውያን በሸለለቆው ይኖራሉ፡፡) ነገ ተመልሳችሁ በሸምበቆው ባህር በኩል ወደ ምድረ በዳው ሂዱ፡፡” 26 ህዌ ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፣ 27 ”እኔን የሚነቅፈውን ይህን ክፉ ማህበረሰብ እስከ መቼ እታገሳለሁ የእስራኤል ሰዎች በእኔ ላይ ሲያጉረመርሙ ሰምቻለሁ፡፡ 28 እንዲህ በላቸው ‘እኔ ሕያው ነኝ’ ይላል ያህዌ፣ ‘እኔ እየሰማሁ፣ የተናገራችሁትን፣ ያንኑ አደርግባችኋለሁ፡፡ 29 በድናችሁ በዚህ ምድረ በዳ ይወድቃል፣ እናንተ በእኔ ላይ ያጉረመርማችሁ ሁላችሁም፣ በህዝብ ቆጠራው የተቆጠራችሁ ሃያ አመትና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላችሁ ሰዎች ሁሉ ትሞታላችሁ፡፡ 30 መኖሪያችሁ ትሆን ዘንድ እንደምሰጣችሁ ቃል ወደገባሁላችሁ ምድር ከዮፍኒ ልጅ ከካሌብና ከነዌ ልጅ ከኢያሱ በስተቀር ከእናንተ አንዳችሁም አትገቡም፡፡ 31 ነገር ግን ተጠቂ ይሆናሉ ያላችኋቸው ትንንሽ ልጆቻችሁን፣ እኔ ወደ ምድሪቱ አስገባቸዋለሁ፡፡ እናንተ የናቃችኋትን ምድር እነርሱ ይገቡባታል! 32 እናንተ ግን፣ በድናችሁ በዚህ ምድረ በዳ ይወድቃል፡፡ 33 ልጆቻችሁ ለአርባ አመታት በምድረዳ ይንከራተታሉ፡፡ በረሃው ሁላችሁንም እስኪገድላችሁ ድረስ፣ እነርሱ እናንተን የአመጽ ድርጊቶች ዋጋ ይከፍላሉ፡፡ 34 ምድሪቱን በተመለከታችሁባቸው አርባ ቀናት ልክ፣ ለአርባ አመታት ስኃጢአታችሁ መከራ ትቀበላላችሁ - ለእያንዳንዱ ቀን አንድ አመት፣ እናም የእኔ ጠላት መሆን ማለት ምን ማለት እንደሆነ ታውቃላችሁ፡፡ 35 እኔ ያህዌ፣ ይህንን ተናግሬያለሁ፡፡ በእኔ ላይ በተነሱ በዚህ ክፉ ማህበረሰብ ላይ በእርግጥ ይህን አደርጋሁ፡፡ በዚህ ምድረ በዳ ይጠፋሉ፡፡ በዚህ ስፍራ ይሞታሉ፡፡” 36-37 ስለዚህ ሙሴ ምድሪቱን እንዲያዩ የላካቸው ሰዎች ሁሉ በያህዌ ፊት በወረርሽኝ አለቁ፡፡ እነዚህ ሰዎች ስለምድሪቱ መጥፎ ወሬ ይዘው የተመለሱ ነበሩ፡፡ ይህም መላው ማህበረሰብ በሙሴ ላይ እንዲያጉረመርም አደረገ፡፡ 38 ምድሪቱን ለማየት ከሄዱት ሰዎች መሀል፣ የነዌ ልጅ ኢያሱና የዩፎኒ ልጅ ካሌብ ብቻ በህይወት ቀሩ፡፡ 39 ሙሴ እነዚህን ቃላት ሁሉ ለእስራኤል ሰዎች ሲናገር፣ በጥልቅ አዘኑ፡፡ 40 ማልደው ተነስተው ወደ ተራራው ጫፍ ወጥተው እንዲህ አሉ፣ “እነሆ፣ አሁን በዚህ አለን፣ ደግሞም ያህዌ ቃል ወደገባልን ስፍራ እንሄለን፣ እኛ በድለናል፡፡” 41 ነገር ግን ሙሴ እንዲህ አለ፣ “ለምን አሁን የያህዌን ትእዛዝ ትሽራላችሁ ድል አይቀናችሁም፡፡ 42 አትውጡ፣ ምክንያቱም በጠላቶቻችሁ እንዳትሸነፉ ሊጠብቃችሁ ያህዌ ከእናንተ ጋር አይደለም፡፡ 43 በዚያ አማሌቃዊያንና ከነዓናዊያን አሉ፣ እናንተም በሰይፍ ታልቃላችሁ ምክንቱም ያህዌን ከመከተል ፊታችሁን መልሳችኋል፡፡ ስለዚህ እርሱ ከእናንተ ጋር አይሆንም፡፡” 44 እነርሱ ግን ወደ ተራራማው አገር ለመሄድ በድፍረት ተነሱ፣ ሆኖም፣ ሙሴም ሆነ የያህዌ የቃል ኪዳኑ ታቦት ከሰፈር አብሯቸው አልወጣም፡፡ 45 ከዚያ አማሌቃዊያን ወርደው መጡ፣ እንደዚሁም በተራሮቹ የሚኖሩ ከነዓናዊያን መጡባቸው፡፡ እነርሱም እስራኤላውያንን አጠቋቸው እስከ ሔርማ መንገድ ድረስ አሳደዷቸው፡፡



Numbers 14:1

እግዚአብሔር በሰይፍ እንሞት ዘንድ ወደዚች ምፍር ለምን ያገባናል?

እዚህ ላይ ሰዎቹ ጥያቄ የሚያነሱት እግዚአብሔር በአግባቡ እንዳልያዛቸው ለመግለፅ ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በሠይፍ እንድንገደል ለማድረግ ሲል ብቻ እግዚአብሔር ወደዚህ ሥፍራ ሊያመጣን አይገባም ነበር” (ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በሠይፍ ለመገደል

እዚህ ላይ“ሠይፍ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በሠይፍ መሞትን ወይም በጦርነት ውስጥ መሞትን ነው፡፡ “ሰዎች በሠይፍ ሲያጠቁን መሞት”ወይም “በጦርነት ውስጥ መሞት”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ ግብፅ መመለስ አይሻለንምን?

ሰዎቹ ይሄንን ጥያቄ የሚጠይቁት ሌሎች ሰዎችም ወደ ግብፅ ብንመለስ ይሻለናል ብለው በሃሣባቸው እንዲስማሙላቸው ለማድረግ ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ከነዓንን ለማሸነፍ ከምንጥር ይልቅ ወደ ግብፅ ብንመለስ ይሻለናል”

Numbers 14:4

እርስ በእርሣቸው ተነጋገሩ

ይሄ የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡

በግምባራቸው ወደቁ

“ፊታቸው መሬቱን ነክቶ ሰገዱ”ሙሴና አሮን ይህንን ያደረጉት ራሣቸውን በእግዚአብሔር ፊት ማዋረዳቸውን ለማሣየት ነበር፡፡ሕዝቡ በእግዚአብሔር ላይ ስላመፀ ሊቀጣቸው ይችል ይሆናል ብለው በመስጋታቸው ነበር፡፡“በእግዚአብሔር ፊት ትህትናን ለማሣየት ፊትን ወደ መሬት መድፋት”ወይም “ወደ እግዚአብሔር ለመፀለይ ፊትን ወደ መሬት መድፋት”(ተምሣሌታዊ ደርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:6

ነዌ…ዮፎኒ

እነዚህ የሰው ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሰላዮቹ ጋር የነበሩት አንዳንድ ሰዎች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴ ከላካቸው መካከል አንዳንድ ሰዎች” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ልብሣቸውን ቀደዱ

ልብስን መቅደድ የሚመለክተው አንድ ሰው ችግር ላይ እንዳለና በርቱ ለቅሶ እያለቀሰ የሚገኝ መሆኑን ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት)

ወተትና ማር ወደምታፈስሰው

ምድሪቱ ለእንስሳትና ለዕፅዋት ተስማሚ መሆኗን ለመግለፅ ከእነዚያ እንስሳት የሚገኘው ወተትና ማር ልክ በምድሪቱ ላይ እንደሚፈስስ ዓይነት ነገር አድርገው ይገልፁታል፡፡ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 1፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ከብቶችን ለማርባትና ለእህል ዕድገት እጅግ የሚያመች ሥፍራ ነው”ወይም “እጅግ ለም የሆነ መሬት ነው” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:9

የማያያዣ ዓረፍተ ነገር

ኢያሱና ካሌብ ለሕዝቡ መናገራቸውን ይቀጥላሉ፡፡

እንደ አንጀራ ይሆኑልናል

ኢያሱና ካሌብ ጠላቶቻቸውን ማጥፋት እንጀራን እንደመብላት ያህል ቀላል እንደሆነ ይናገራሉ፡፡“ምግብን የመብላት ያህል በቀላሉ እናጠፋቸዋለን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

ጥላቸው ከላቸው ተግፍፏል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ጥላቸውን ከላያቸው ላይ ይገፍፋል” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

መከላከያቸው

“መከላከያቸው” የሚለው አሕፅሮተ ሥም “መከላከል”በሚለው ሥም(ሰዋሰው)ሊገለፅ ይችላል፡፡ (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:11

ይህ ሕዝብ እስከ መቼ ይንቀኛል?በፊቱስ ባደረግሁት ተአምራት ሁሉ እስከ መቼ አያምንብኝም?....እነርሱ?

እግዚአብሔር ይህንን ጥያቄ የጠየቀው መቆጣቱን ለመግለፅና ሕዝቡን በሚመለከት ትዕግሥቱ ማለቁን ለማሣየት ነው፡፡እነዚህ በድርጊቶች ሊገለፁ ይችላሉ፡፡“ይሄ ሕዝብ ለብዙ ጊዜ ጠልቶኛል፡፡በፊቱ ባደረግሁት ተአምራት ሁሉ አላመነብኝም....እነርሱ፡፡(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ከርስታቸው አጠፋቸው ዘንድ

“የእኔ ሕዝበ እንዳልሆኑ እቆጥራቸዋለሁ”በአንዳንድ ቅጂዎች ትርጓሜ መሠረት ደግሞ ሊያጠፋቸው እንደፈለገ የሚያመለክት ሊሆንም ይችላል፡፡

የራስህን ነገድ ፍጠር

እዚህ ላይ “የራስህን የሚለው ቃል ነጠላ ስለሆነ የሚያመለክተው ሙሴን ነው፡፡(አንተ የሚለው ቃል በተለያየ መንገድ የሚገለፅበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:13

ፊት ለፊት ትተያያለህ

ለዚህ ትርጉም ሊሆኑ የሚችሉት 1/ሙሴ እግዚአብሔር ራሱን ለሕዝቡ የሚገልፅበትን ሁኔታ ልክ ፊቱን እንዲያዩ እንደፈቀደላቸው አድርጎ ያቀርበዋል 2/ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን የጠበቀ ግንኙነት ለመግለፅ ልክ እግዚአብሔር ለሙሴ በሚናገርበት ወቅት ፊቱን እንደተመለከተ ዓይነት አድርጎ ተነግሯል፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንተ ለእኔ የምትናገረው በቀጥታ ነው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:15

እንደ አንድ ሰው

ሁሉንም በአንድ ጊዘ መግደልን ልክ አንድን ሰው እንደመግደል ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ሁሉንም በአንድ ጊዜ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:17

የቃል ኪዳንህ ታማኝነት የተትረፈረፈ

“ታማኝነት”የሚለው አሕፅሮተ ቃል “ታማኝ”ወይም “በታማኝነት”ተብሎ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ዘወትር ለቃል ኪዳኑ ታማኝ የሆነ”ወይም “ሕዝቡን ዘወትር በታማኝነት ያፈቅራል” (አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ኃጢአተኞችን ከቶ የማያነፃ

“እውነትም ኃጢአተኛ የሆኑ ሰዎችን ይቅር አይልም” የሰዎችን ኃጢአት ማስወገድ የሚለው ቃል ለመቀጣት ፈቃደኛ ላለመሆናቸው ምሣሌያዊ አነጋገር ነው፡፡እግዚአብሔር የበደለኞችን ኃጢአት ይቅር አይልም፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የአባቶችን ቅጣት በልጆች ላይ የሚያመጣ

እዚህ ላይ መቅጣት የሚለው ሃሣብ የተገለፀው ልክ አንድ ቁሣቁስ መጥቶ በሕዝብ ላይ እንደሚቀመጥ ዓይነት ተደርጎ ነው፡፡“በበደሉ ሰዎች ኃጢአት ምክኒያት የበደሉትን ሰዎች ትውልድ ሲቀጣ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:20

ምድር ሁሉ በእኔ ክብር ይሞላል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ክብሬ ምድርን ሁሉ ይሞላል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ተፈታተኑኝ

“መፈታተኑን አላቋረጡም”

አሥር ጊዜ

እዚህ ላይ አሥር ጊዜ ሲባል ለብዙ ጊዜያት ለማለት ነው፡፡“ለብዙ ጊዜ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ድምፄን አልሰሙም

እዚህ ላይ “መስማት”የሚለው ቃል የሚመለክተው መታዘዝን ሲሆን የእግዚብሔር ድምፅ የሚለው ቃል የሚያመለክተው ደግሞ የእርሱን ንግግር ነው፡፡“የተናገርኩትን ነገር አልታዘዛችሁም” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:23

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ሌላ መንፈስ ከእርሱ ጋር ስላለ

እዚሀ ላይ “መንፈስ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አስተሳሰቡን ነው፡፡ካሌብ እግዚአብሔርን ለመታዘዝ ፈቃደኛ ነበር፡፡አስተሳሰቡ ምን እንደነበረ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“የተለየ አስተሳሰብ የነበረው በመሆኑ”ወይም “እግዚአብሔርን ለመታዘዝ ፈቃደኛ ስለነበረ” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውንና ግልፅ የሆነ ትግበራ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:26

የሚያጉረመርምብኝን ይህን ክፉ ሕዝብ እስከ መቼ እታገሰዋለሁ?

እግዚአብሔር ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው በሕዝቡ ላይ ያለው ትዕግሥት በመሟጠጡ ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለብዙ ጊዜ ሲያጉረመርምብኝ የኖረውን ይህንን ማህበረሰብ ታግሼዋለሁ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤልን ልጆች ማጉረምረም ሰማሁ

“ማጉረምረም”የሚለው አሕፅሮተ ሥም በሥም(ሰዋሰው) መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእሥራኤል ሕዝብ ሲያጉረመርም ሰምቻለሁ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:28

በጆሮዬ እንደተተናገራችሁት

“ስትናገሩ እንደሰማኋችሁ”

በድኖቻችሁ ይወድቃሉ

የበድኖቻቸው መውደቅ የሚያመለክተው የሚሞቱ መሆኑን ነው፡፡“ትሞታላችሁ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የተቆጠራችሁ ሁሉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ቆጠራ በተካሄደበት ወቅት ሙሴ የቆጠራችሁ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሃያ ዓመት ጀምሮ ከዚያም በላይ

“ሃያ ዓመትና ከዚያ በላይ የሆኑ”

Numbers 14:31

በድኖቻችሁ ይወድቃሉ

የበድኖቻቸው መውደቅ የሚያመለክተው የሚሞቱ መሆኑን ነው፡፡“ትሞታላችሁ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ልጆቻችሁ በምድረ በዳ እረኞች ይሆናሉ

አንዳንድ የትርጉም ቅጂዎች “ልጆቻችሁ በምድረ በዳ ይቅበዘበዛሉ”የሚለውን ሃሣብ ይመርጡታል፡፡ይሄ የሆነበት ምክኒያት ከብቶቹ የሚግጡት ሣር እስከሚያገኙ ድረስ እረኞቹ ከቦታ ቦታ ይዘዋወሩ ስለነበረ ነው፡፡

የሥራችሁን ውጤት መሸከም ይኖርባቸዋል

“ከድርጊታችሁ ፍሬ የተነሣ ሊሰቃዩ ይገባል”ወይም “ከእናንተ ድርጊት የተነሣ እነርሱ ሊሰቃዩ ይገባል”

በድኖቻችሁ እስከጠፉ ድረስ

በድን ሬሣ ነው፡፡በድኖቻችሀ እስኪጠፉ ድረስ የሚለው ቃል የሚያመለክተው አንድ ሰው ሣይቀር የሚሞት መሆኑን ነው፡፡“ከእናንተ የመጨረሻው ሰው እስከሚሞት ድረስ”ወይም “ሁላችሁም እስክትሞቱ ድረስ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:34

ኃጢአታችሁን ትሸከማላችሁ

“በኃጢአታችሁ ፍሬ ተሰቃዩ”ወይም “ከኃጠአታችሁ የተነሣ ተሰቃዩ”

ፈፅመው ይቆረጣሉ

ይሄ ምናልባት በሕይወት አይኖሩም ለማለት ሊሆን ይችላል፡፡“ፍፃሜያቸው ይሆናል”ወይም “ይጠፋሉ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውንና ግልፅ የሆነ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:36

ክፉ ወሬ ያወሩ እነዚያ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት በመቅሠፍት ሞቱ

“በእግዚአብሔር ፊት በመቅሠፍት”የሚለው ቃል የሚያመለከተው በእግዚአብሔር የተመቱ መሆኑን ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ስለምድሪቱ ከፉ ወሬ ያመጡትን ሰዎች በእግዚአብሔር ተቀስፈው ሞቱ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውንና ግልፅ የሆነ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:39

እነሆ መጣን

ይህንን ነገር የተናገሩት ሃሣባቸውን መለወጣቸውንና ከአንድ ቀን በፊት ማድረግ የነበረባቸውን ነገር ለማድረግ መፈለጋቸውን አፅንኦት ለመሥጠት ነው፡፡የእናንተ ቋንቋ ይህንን የማብራራት የራሱ መንገድ ሊኖረው ይችላል፡፡

Numbers 14:41

የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ለምን ትተላለፋላችሁ?

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የጠየቀው የእሥራኤልን ሕዝብ ለመገሰፅ ነው፡፡ይሄ አሕፅሮተ ሥም በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ እንደገና መተላለፍ የለባችሁም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር በእናንተ መካከል አይደለም

እነርሱን ማገዝ ከእነርሱ ጋር እንደመኖር ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እግዚአብሔር አይረዳችሁም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በጠላቶቸችሁ ፊት እንዳትወድቁ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ጠላቶቻችሁ ድል እንዳይነሷችሁ ለመከላከል” ወይም “በጠላቶቻችሁ ላይ ድልን እንድታገኙ ለማድረግ” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በሰይፍ ትወድቃላችሁ

እዚሀ ላይ “ሠይፍ”የሚያመለክተው ጦርነትን ነው፡፡“በጦርነት ውስጥ ትሞታላችሁ”ወይም “ከእነርሱ ጋራ ስትዋጉ ይገድሏችኋል” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን ከመከተል ተመልሳችኋልና

እግዚአብሔርን መታዘዝ እርሱን እንደ መከተል ተደርጎ የተገለፀ ሲሆን የሚናገረውን ቃል አለመፈፀም ደግሞ ከእርሱ እንደመመለስ ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እግዚአብሔርን መታዘዝ አቁማችኋል”ወይም “እግዚአብሔርን ላለመታዘዝ ወስናችኋል” “(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)”

ከእናንተ ጋር አይሆንም

እነርሱን ማገዝ ከእነርሱ ጋር እንደመኖር ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡“አይረዳችሁም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 14:44

እነርሱ ግን ወደ ተራራው ራስ ሊወጡ ደፈሩ፡፡“እግዚአብሔር ያልፈቀደው ነገር ቢሆንም እነርሱ ግን ወደ ተራራው ራስ ሊወጡ ደፈሩ፡፡”

እነርሱ ግን ወደ ተራራው ራስ ሊወጡ ደፈሩ፡፡“እግዚአብሔር ያልፈቀደው ነገር ቢሆንም እነርሱ ግን ወደ ተራራው ራስ ሊወጡ ደፈሩ፡፡”

በተራራማው አገር

አብዛኛው የእሥራኤል ምድር ከፍታ ያለው ሥፍራ ነው፡፡የእሥራኤል ልጆች ከነዓናውያንን ለመውጋት የዮርዳኖስን ወንዝ በተሻገሩበት ወቅት ወደ ከነዓን ምድር ውስጥ ዘልቀው ለመግባት መውጣት የሚኖርባቸው ተራራዎች ነበሩ፡፡


Chapter 15

1 ከዚያ ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 2 “ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‘ያህዌ ለእናንተ ወደሚሰጣችሁ ወደ ምትኖሩባት ምድር ስትገቡ 3 ለእርሱ በእሳት መስዋዕት ስታቀርቡ፣ የሚቃጠል መስዋዕት ወይም ስዕለት ስታመጡ ወይም የበጎ ፈቃድ ስጦታ፣ ወይም በባዕላቶቻችሁ ለያህዌ ስጦታዎችን ከከብቶች ወይም ከመንጋችሁ ስታቀርቡ 4 ለያህዌ መስዋዕቱን የሚያቀርበው ሰው፣ በአንድ አራተኛ ኢን ዘይት የተለወሰ የኢፍ አንድ አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል መስዋዕት ያቅርብ፡፡ 5 እንዲሁም የኢን አንድ አራተኛ ወይን ለመጠጥ መስዋዕት አቅርቡ፡፡ ይህን ከሚቃጠል መስዋዕት ጋር ወይም እያንዳንዱ ጠቦት ሲቀርብ አድርጉት 6 አውራ በግ የምታቀርቡ ከሆነ፣ የኢፍ ሁለት አስረኛ መልካም ዱቄት በአንድ ሶስተኛ ኢን ዘይት የተለወሰ የእህል ቁርባን አቅርቡ፡፡ 7 ለመጠጥ መስዕት፣ የኢን አንድ ሶስተኛ ወይን አቅርቡ፡፡ ይህ ለያዌ ጣፋጭ መዓዛ ይሆናል፡፡ 8 ለሚቃተል መስዋዕት በሬ፣ ወይም ስዕለት ለማድረስ መስዋዕት ወይም ለያህዌ የህብረት መስዋዕት ስታዘጋጁ 9 ከበሬው ጋር በግማሽ ኢን ዘይት የተለወሰ የኢፍ ሶስት አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን አቅርቡ፡፡ 10 ለያዌ ጣፋጭ መዓዛ እንዲሆን ለመጠጥ ቁርባን የኢን ግማሽ ወይን፣ በእሳት የሚረብ መስዋዕት አቅርቡ፡፡ 11 እያንዳንዱ በሬ፣ እያንዳንዱ አውራ በግ፣ እና እያንዳንዱ ወንድ ጠቦት በግ ወይም ጠቦት ፍየል ሲቀርበ በዚህ አይት ይሁን፡፡ 12 እያንዳንዱ የምታዘጋጁት መስዋዕት እና ስጦታ እዚህ እንደተገለፀው ይቅረብ፡፡ 13 ማንም ሰው ለያህዌ ደስ የሚያሰኝ መዓዛ ለማቅረብ በእሳት የተዘጋጀ መስዋዕት ሲያመጣ፣ የአገር ተወላጅ የሆነ እስራኤላዊ ሁሉ እነዚህን ነገሮች በዚህ መንገድ ያድርግ፡፡ 14 መጻተኛው ከእናንተ ጋር ቢኖር፣ ወይም በእናንተ ትውልድ መሀል የሚኖር ማናቸውም ሰው፣ ለያህዌ መልካም መዓዛ ለማቅረብ በእሳት የተዘጋጀ መስወዕት ያድርግ፡፡ እርሱ እናንተ እንደምታደርጉት ያድርግ፡፡ 15 ለማህበረሰቡ እና ከእናንተ ጋር ለሚኖር መጻተኛ ተመሳሳይ ህግ ይሁን፣ ይህ በትውልዳች ሁሉ የፀና ህግ ይሁን፡፡ እናንተ እንደ ታያችሁት፣ ከእናንተ ጋር የሚኖሩ እንግዶች በአንድ አይነት ይታያሉ፡፡ 16 ለእናንተም ሆነ ከእናንተ ጋር ለሚኖሩ መጻተኞች ተመሳሳይ ህግና ደንቦች ተግባራዊ ይደረጋሉ፡፡” 17 ያህዌ ዳግም ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 18 ”ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‘ወደ ማስገባችሁ ምድር በመጣች ጊዜ፣ 19 በምድሪቱ የተመረተውን ምግብ በበላችሁ ጊዜ፣ መስዋዕት መሰዋትና ለእኔ ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 20 ከመጀመሪያው ቡኬታችሁ ከአውድማው የማንሳት መስዋዕት ህብስት አቅርቡ፡፡ በዚህ መንገድ መስዋዕታችሁን አቅርቡ፡፡ 21 በትውልዶች ሁሉ ከመጀመሪያው ቡኬታችሁ የማንሳት መስዋዕት ለእኔ ትሰጣላችሁ፡፡ 22 አንዳንድ ጊዜ ለማድረግ ሳታስቡ ለሙሴ የነገርኩትን እነዚህን ህጎች ሁሉ በተመላለፍና 23 ትዕዛዛትን ለእናንተ መስጠት ከጀመርኩበት ቀን አንስቶ በትውልዳችሁ ቀጣይ ዘመናት በሙሴ በኩል ያዘዝኳችሁን ነገሮች በሙሉ ባታደርጉ ኃጢአት ትሰራላችሁ፡፡ 24 ማህበረሰቡ ሳያውቅ በደል ፈጽሞ ሲገኝ፣ መላው ህብረተሰብ ለያህዌ መልካም መዓዛ እንዲሆን አንድ ወይፈን ለሚቃጠል መስዋዕት ያቀርባል፡፡ ከዚሁ ጋር የእህል ቁርባን እና የመጠጥ ቁርባን እንዲሁም ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል በደንቡ መሠረት ያቅርብ፡፡ 25 ካህኑ ለመላው የእስራኤል ማህበረሰብ ማስተስረያ ያቀርባል፡፡ ኃጢአቱ የተፈፀመው፣ ባለማወቅ ስለሆነ ይቅር ይባላሉ፡፡ ለእኔ በእሳት የተዘጋጀውን መስዋዕታቸውን አቅርበዋልና ይቅር ይባለሉ፡፡ በእኔ ፊት ሳያውቁ ለፈጸሙት ስህተት የኃጢአት መስዋዕታቸውን አቅርበዋልና፡፡ 26 ከዚያ መላው የእስራኤል ማህበረሰብና ከእነርሱ ጋር የሚኖሩ መጻተኞች ይቅር ይባላሉ፣ ምክንያቱም ሁሉም ኃጢአቱን የፈፀሙት ሆን ብለው አይደለም፡፡ 27 አንድ ሰው ሳያውቅ ኃጢአት ቢሰራ ለኃጢአት መስዋዕት የአንድ አመት ሴት ፍየል ያቅርብ፡፡ 28 ካህኑ ሳያውቅ ኃጢአት ለሰራው ሰው በያህዌ ፊት ያስተሰርይለታል፡፡ ያ ሰው ማስተሰርያ ሲደረግ ይቅር ይባላል፡፡ 29 ማናቸውንም ነገር ሁን ብሎ ላላደረገ ተመሳሳይ ህግ ይኑራችሁ፣ በእስራኤል ሰዎች መሀል ለሚኖረው ተወላጅም ሆነ መጻተኛ ተመሳሳይ ህግ ይኑራቸው፡፡ 30 ነገር ግን ራሱን ለመከላከል አንዳች ነገር ያደረገ ሰው፣ የአገር ተወላጅም ይሁን መጻተኛ እኔን ያቃልላል፡፡ ስለዚህ ያ ሰው ከወገኖቹ ተለይቶ ይጥፋ፡፡ 31 ምክንቱም እርሱ ቃሌን ንቋል ደግሞም ትዕዛዛቴን ተላልፏል፣ ያ ሰው ሙሉ ለሙሉ ከህዝቡ ተለይቶ ይጥፋ፡፡ ኃጢአቱ በራሱ ላይ ይሆናል፡፡” 32 የእስራኤል ህዝቦች በምድረ በዳ በነበሩበት ጊዜ፣ አንድ ሰው በሰንበት ቀን እንጨት ሲለቅም አገኙት፡፡ 33 ያገኙት ሰዎች ወደ ሙሴ፣ ወደ አሮንና ወደ መላው ማህበረሰብ አቀረቡት፡፡ 34 በእርሱ ላይ ምን መደረግ እንዳለበት የታወቀ ህግ ስላልበረ በጥበቃ ሥር አቆዩት፡፡ 35 ከዚያ ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “በእርግጥ ሰውየው መገደል አለበት፡፡ መላው ማህበረሰብ ከሰፈር ውጭ በድንጋይ ይውገረው፡፡” 36 ስለዚህም መላው ማህበረሰብ ሰውየውን ከሰፈር ውጭ አውጥተው ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው እስኪሞት ድረስ ወገሩት፡፡ 37 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 38 “ለእስራኤል ትውልዶች በየለብሳቸው ጠርዝ ዘርፍ እንዲያስሩ ንገራቸው፣ ዘርፎቹን በእያንዳንዱ ጠርዝ በሰማያዊ ገመድ እንዲያንጠለጥሉ እዘዛቸው፡፡ በሚቀጥሉት ትውልዶቻቸው ሁሉ ይህን ያድርጉ፡፡ 39 ይህንን ስትመለከቱ፣ በትዕዛዛት ሁሉ፣ እንድትሄዱ፣ የራሳችሁን ልቦናና እይታ ሳትከተሉ ቀድሞ ታደርጉት ከነበረው መንፈሳዊ አመንዝራነት ለመመለስ ይህ ለእናንተ ልዩ ማስታወሻ ይሆናችኋል፡፡ 40 ትዕዛዛቶቼን ሁሉ እንድትጠብቁና አስተዋዮች እንድትሆኑ ይህን አድርጉ፣ ደግሞም ቅዱሳንና ለእኔ ለአምላካችሁ የተለያችሁ ትሆናላች፡፡ 41 አምላካችሁ እሆን ዘንድ፣ ከግብጽ ምድር ያወጣኋችሁ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡ እኔ ያህዌ አምላካችሁ ነኝ፡፡”



Numbers 15:1

አጠቃላይ መረጃ

ዘኁልቁ 15፤1-32 ድረስ ያለው ክፍል ሙሴ ለእሥራኤላውያን እንዲናገራቸው እግዚአብሔር የተናገረውን የሚገልፅ ነው፡፡

ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ ታደርጉ ዘንደ ከበሬ ወይም ከበግ መንጋ

“ከበሬ ወይም ከበግ መንጋ ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታን ማቅረብ”እግዚአብሔር በጣፋጩ ሽታ ደስ መሰኘቱ የሚያመለክተው መሥዋዕቱን በሚያቀርበው ሰው መደሰቱን ነው፡፡“ከበሬ ወይም ከበግ መንጋ ጣፋጭ ሽታን በማቅረብ እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:4

የሚቃጠል መሥዋዕት

ይሄ የሚያመለክተው በኦሪት ዘኁልቁ 15፡3 የተጠቀሱትን መሥዋዕቶች ነው፡፡

ከአሥር አንድ እጅ የሆነ መሥፈሪያ

መስፈሪያ የመለኪያ ዓይነት ሲሆን ከ22 ሊትር ጋር እኩል ነው፡፡“2 ሊትር ያህል”ወይም “ሁለት ሊትር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

የኢን መሥፈሪያ አራተኛ እጅ

ኢን የመለኪያ ዓይነት ሲሆን ከ3.7 ሊትር ጋር እኩል ነው፡፡“1 ሊትር ያህል”ወይም “አንድ ሊትር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:6

መሥፈሪያ ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

መስፈሪያ የመለኪያ ዓይነት ሲሆን ከ22 ሊትር ጋር እኩል ነው፡፡“4 ሊትር ያህል”ወይም “አራት ተኩል ሊትር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

የኢን መሥፈሪያ ሲሶ

ኢን የመለኪያ ዓይነት ሲሆን ከ3.7 ሊትር ጋር እኩል ነው፡፡“አንድ ሊትር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ ይሆናል

“እግዚአብሔርን የሚያስደስት ሽታ ይወጣዋል” እግዚአብሔር በጣፋጩ ሽታ ደስ መሰኘቱ የሚያመለክተው መሥዋዕቱን ባቀረበው ሰው ሐሴት ማድረጉን ነው፡፡“እርሱን መሥዋዕት በማድረግ እግዚአብሔርን ታስደስታላችሁ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:8

ከመሥፈሪያው ከአሥር እጅ ሶስት እጅ

ይህንን ወደ ዘመናዊ መለኪያ ልትለውጡት ትችላላችሁ፡፡“ስድስትና አንድ ከግማሽ ሊትር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

ግማሽ ኢን

ይህንን ወደ ዘመናዊ መለኪያ ልትለውጡት ትችላላችሁ፡፡“ሁለት ሊትር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሣት የተደረገ

“በመሠዊያው ላይ የምታቃጥሉት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታን ለማቅረብ

“እግዚአብሔርን የሚያስደስት ሽታ ማቅረብ” በቅን ልብ መሥዋዕትን በሚያቀርብ ሰው እግዚአብሔር መደሰቱን ለመግለፅ ልክ እግዚአብሔር በመልካም ሽቱ መሥዋዕት እንደሚደሰት ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እርሱን በማቅረብ እግዚአብሔርን ማስደሰት፡፡”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:11

ሊደረግ ይገባል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እናንተ ልታደርጉት ይገባል” (ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በተገለፀው መሠረት እንዲሁ መደረግ ይኖርበታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡በተናገርኩት መሠረት መፈፀም ይኖርባችኋል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሳት የተደረገ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእሣት ላይ የሚያቀጥሉትን”

ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ የሚሆንን ነገር ለማቅረብ

“ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ ሽታ ለማቅረብ” የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር በቅን ልብ መሥዋዕትን በሚያቀርብ ሰው መደሰቱን ለመግለፅ ልክ እግዚአብሔር በመልካም ሽቱ መሥዋዕት እንደሚደሰት ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እርሱን በማቅረብ እግዚአብሔርን ማስደሰት፡፡”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:14

ቁርባንን በእሣት ማቅረብ ይኖርበታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በመሠዊያው ላይ ቁርባንን ማቃጠል ይኖርበታል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ የሚሆንን ነገር ለማቅረብ

“እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሽታ ለማቅረብ”የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር በቅን ልብ መሥዋዕትን በሚያቀርብ ሰው መደሰቱን ለመግለፅ ልክ እግዚአብሔር በመልካም ሽቱ መሥዋዕት እንደሚደሰት ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እርሱን በማቅረብ እግዚአብሔርን ማስደሰት፡፡”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በእናንተም መካከል ለሚቀመጥ መፃተኛ አንድ ሥርዓት ይሆናል

ለዚህ ትርጉም ሊሆኑ የሚችሉት1/ “እናንተና በመካከላችሁ ያሉት መፃተኞች በእግዚአብሔር ፊት እኩል ናችሁ”ወይም “እናንተንም ሆነ መፃተኛውን የሚገዛው ሕግ ተመሳሳይ ነው”

እናንተ እንደምታደርጉት እንዲሁ በእግዚአብሔር ፊት ያደርጋል

እናንተ እንደምታደርጉት እንዲሁ በእግዚአብሔር ፊት የሚያደርጉበት ምክኒያት በእግዚአብሔር ፊት እንደ እሥራኤላውያን መሆን ያለባቸው በመሆኑ ነው፡፡ይሄ የሚያመለክተው ሕጎቹን ሁሉ እንደ እሥራኤላውያን መጠበቅ አለባቸው ማለት ነው፡፡እናንተ እንደምታደርጉት ማድረግና ሕጎቹንም ሁሉ መጠበቅ ይኖርባቸዋል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:17

በምድሪቱ ውስጥ ያለውን እንጀራ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ምድሪቱ የምታበቅለው እንጀራ”ወይም “እናንተ በምድሪቱ ውስጥ የምታመርቱት እንጀራ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:20

መጀመሪያ ከምታደርጉት ሊጥ

ለዚሀ ትርጉም ሊሆኑ የሚችሉት 1/በመከር ወቅት የሚሰበስቡት የመጀመሪያው ሰብል ወይም 2/በመጀመሪያ ከሚያገኙት ሰብላቸው የሚሰሩት ሊጥ (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

እንጎቻ

እንጎቻ ተብሎ መጠራቱ የሚያመለክተው ሊጡን በመጀመሪያ መጋገር ያለባቸው መሆኑን ነው፡፡

እንደ ማንሣት ቁርባን ማቅረብ

“ማንሣት”የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው እንደ ሥጦታ መቅረቡን ነው፡፡“እንደ ሥጦታ ማቅረብ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከአውድማ እንደሚነሣ ቁርባን

ሥጦታው ከአውድማ ነው ተብሎ የተገለፀው የእህል ሥጦታቸውን ከሌላው ሰብል ለይተው የሚያስቀምጡበት ሥፍራ አውድማ በመሆኑ ነው፡፡

Numbers 15:22

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ሙሴ ለእሥራኤል ሕዝብ መናገር ስላለበት ነገር መናገሩን ይቀጥላል፡፡

አጠቃላይ መረጃ

እዚህ ላይ “እናንተ” የሚለው ቃል የሚመለክተው እሥራኤላውያንን ነው፡፡

ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ የሚሆንን ነገር ለማቅረብ

“እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሽታ ለማቅረብ” የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር በቅን ልብ መሥዋዕትን በሚያቀርብ ሰው መደሰቱን ለመግለፅ ልክ እግዚአብሔር በመልካም የሽቱ መሥዋዕት እንደሚደሰት ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ እርሱን በማቅረብ እግዚአብሔርን ማስደሰት፡፡”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን መደረግ ይኖርበታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ማድረግ ይኖርባችኋል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ ሕጉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሕጉ እንደሚያዘው”ወይም “ሕጉን ሳወጣ ባዘዝኩት መሠረት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:25

ይሰረይላቸዋል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ይቅር እላቸዋለሁ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሣት የቀረበ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእሣት የሰሩት”ወይም “በመሠዊያው ላይ ያቃጠሉት”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእሥራኤል ልጆች ማህበር ሁሉ ስርየት ይደረግላቸዋል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእሥራኤልን ልጆች ማህበር ሁሉ ይቅር እላቸዋለሁ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:27

የአንድ ዓመት እንስት ፍየል

“አንድ ዓመት የሞላው ፍየል”

መሥዋዕት በሚቀርብበት ወቅት የዚያ ሰው ኃጢአት ይሰረይለታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ካህኑ መሥዋዕትን በሚያቀርብበት ወቅት የዚያን ሰው ኃጢአት ይቅር እላለሁ”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:30

ያም ሰው ከሕዝቡ መካከል ተለይቶ ይጥፋ

“ተለይቶ ይጥፋ” የሚለው ምሣሌያዊ አነጋገር ቢያንስ ሶስት ሃሣቦችን በውስጡ አዝሏል፡፡1/“የራሱ ሕዝብ ሊያባርረው ይገባል”2/“ከእሥራኤል ሕዝብ እንደ አንዱ አልቆጥረውም” “የራሱ ሕዝብ ሊገድለው ይገባል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ትዕዛዜን ሰበረ

ትዕዛዝን አለመፈፀም አንድን ነገር እንደመስበር ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ትዕዛዜን ለመፈጸም ፈቃደኛ አልሆነም” ወይም “ያዘዝኩትን ነገር አልፈፀመም”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ኃጢአቱ በእርሱ ላይ ይሆናል

እዚህ ላይ “ኃጢአት” የሚለው ቃል የሚያመለክተው 1/ለተሰራው ኃጢአት የሚፈረድበትን ቅጣት2/በዚያ ኃጢአት ምክኒያት የደረሰ በደል፡፡ኃጢአት 1/ለመቀጣትና 2/ለበደል ምሣሌያዊ አነጋገር ነው፡፡ “1/በሰራው ኃጢአቱ ምክኒያት እቀጣዋለሁ” ወይም 2/ “እንደ በደለኛ እቆጥረዋለሁ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውንና (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ))

Numbers 15:32

በእርሱ ላይ ሊወሰድ የሚገባው እርምጃ አልታወቀም ነበር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በእርሱ ላይ ስለሚወሰደው እርምጃ አልተናገረም ነበር”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:35

ሰውዬው ፈፅሞ ይገደል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰውዬውን በእርግጥም መግደል ይኖርባችኋል”ወይም “ሰውዬው በእርግጥ መሞት ይኖርበታል”(ገቢራዊና ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:37

የእሥራኤል ትውልዶች

“የእሥራኤል ሕዝብ”

ተግባራዊ ለማድረግ

“እነርሱን ለመታዘዝ”

የልባችሁንና የዓይኖቻችሁን ፈቃድ እንዳትመለከቱ

እዚህ ላይ “መመልከት”የሚለው ቃል ማሰብ ለሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡ልብ አንድ ሰው የሚሻውን ነገር የሚያመለክት ሲሆን ዓይን ደግሞ አንድ ሰው የሚያየውንና የሚፈልገውን ነገር ያመለክታል፡፡“የምትፈልጉትን ነገር ሁሉ እንዳታስቡ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

እርስዋን በመከተል ያመነዘራችሁበትን

ልባቸው ያሻውን ነገር እያደረጉ እግዚአብሔርን ያለመታዘዛቸውን ሁኔታ አንዲት ሴት ለባልዋ ታማኝ ካለመሆኗ የተነሣ ከሌላ ሰው ጋር ዝሙት እንደምትፈፅም ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡ይሄ አሣፋሪ ድርጊት ስለመሆኑ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“በሚያሣፍር ሁኔታ ለእኔ ታማኝ አልሆናችሁም”ወይም “ከመታዘዝ ይልቅ እነዚሀን ነገሮች ታደርጋላችሁ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን፤በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 15:40

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ሙሴ ለእሥራኤል ሕዝብ መናገር የሚኖርበትን ነገር መንገሩን ቀጥሏል፡፡ “እናንተ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡

በልባችሁ ላይ እንዲታይ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“ማስታወስ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝ

ይሄ ሐረግ የተደጋገመው አፅንኦት ለመስጠት ሲባል ነው፡፡


Chapter 16

1 የይስዓር ልጅ ቆሬ የቀዓት ልጅ የሌዊ ልጅ፣ ከኤሊያብ ልጆች ከዳታንና አቤሮን ጋር፣ እንዲሁም የፍሬት ልጅ ኦን፣ የሮቤል ትውልዶች ሆነው ተሰበሰቡ፡፡ 2 እነርሱም ከእስራኤል ሌሎች ሰዎች ጋር ሆነው በሙሴ ላይ ተቃውመው ተነሱ፣ የማህበረሰቡ መሪዎች የሆኑ የታወቁ ሁለት መቶ ሀምሳ ሰዎች ተነሱበት፡፡ 3 ሙሴንና አሮንን ለመቃወም በአንድነት ተሰበሰቡ፡፡ ሙሴንና አሮንን እንደዚህ አሏቸው፣ “እናንተ ያለ ልክ አብዝታችሁታል፡፡ መላው ማህበረሰብ ቅዱስ ነው፣ ለያህዌ የተለየ ነው፣ እያንዳንዳቸው ንጹሃን ናቸው፣ ያህዌም በመሀከላቸው ነው፡፡ ለምን ራሳችሁን ከተቀረው የያህዌ ማህበረሰብ ከፍ ታደረጋላችሁ?” 4 ሙሴ ይህንን ሲሰማ፣ በግምባሩ ተደፋ፡፡ 5 ለቆሬና ለእርሱ ወገኖች እንዲህ አላቸው፤ “ማለዳ ያህዌ የእርሱ የሆኑት እነማን እንደሆኑ ይለያል፣ ማን ለእርሱ እንደ ተለየ ይታወቃል፡፡ የመረጠውን ሰው ወደ ራሱ ይለያል፡፡ የመረጠውን ወደ ራሱ ያመጣዋል፡፡ 6 ቆሬና የአንተ ቡድን ሁላች ይህን አድርጉ፡፡ ማጠንት ያዙ 7 ነገ በያህዌ ፊት እሳትና እጣን በላያቸው ጨምሩ፡፡ ያህዌ የሚመርጠው ሰው እርሱ፣ ለያህዌ የተለየ ይሆናል፡፡ እናንተ የሌዊ ትውልዶች ከልክ አልፋችኋል፡፡” 8 እንደገና፣ ሙሴ ቆሬን እንዲህ አለው፣ “አሁን ስማ፣ እናንተ የሌዊ ትውልዶች 9 የእስራኤል አምላክ ከእስራኤል ማህበረሰብ እናተን ለይቶ ወደራሱ ማቅረቡ፣ በያህዌ የማደሪያ ድንኳን እንድታገለግሉ ማድረጉ፣ እነርሱን እንድታገለግሉ በማህበረሰቡ ፊት እናንተን ማቆሙ ለእናንተ ትንሽ ነገር ነውን? 10 እርሱ አንተን፣ የቅርብ ዘመዶችህንና የሌዊ ትውልዶችን ከአንተ ጋር አቅርቧችኋል፣ እናንተ ግን ክህነቱንም እየፈለጋችሁ ነው! 11 አንተና የአንተ ተከታዮች ሁሉ በያህዌ ላይ በአንድ ላይ ተነሳችሁ፡፡ ስለዚህ ለምን እግዚአብሔርን በሚታዘዘው በአሮን ላይ ታጉረመርማላችሁ?” 12 ከዚያ ሙሴ የኤልያብን ልጆች ዳታንንና አብሮንን ጠራቸው፣ እነርሱ ግን እንዲህ አሉ፣ “እኛ ወደዚያ አንመጣም፡፡ 13 እኛን በምድረበዳ ልትገድለን ወተትና ማር ከሚፈስባት ምድር ያወጣኸን ትንሽ ነገር ሆኖ ነውን? አሁን ራስህን በእኛ ላይ ገዢ ማድረግ ትፈልጋለህ! 14 በተጨማሪም፣ እኛን ወተትና ማር ወደምታፈስ ምድር አላመጣኸንም፣ ወይም እርሻዎችንና የወይን ተክሎችን ውርስ አድርገህ አልሰጠኸንም፡፡ አሁን በባዶ ተስፋ ልታታልለን ትፈልጋህ? ወደ አንተ አንመጣም፡፡” 15 ሙሴ እጅግ ተቆጥቶ ነበር፣ ወደ ያህዌ እንዲህ ሲል ጮኸ፣ “መስዋዕታቸውን አትቀበል፡፡ ከእነርሱ አንድ አህያ እንኳን አልወሰድኩም፣ ከእነርሱ አንዳቸውንም አልበደልኩም፡፡” 16 ከዚያ ሙሴ ቆሬን እዲህ አለው፣ “ነገ አንተና የአንተ የሆኑ በያህዌ ፊት ይቅረቡ፤ አንተ፣ እነርሱና አሮን በያህዌ ፊት ቁሙ፡፡ 17 እያንዳንዱ የራሱን ማጠኛ ይያዝና በውስጡ እጣን ይጨምርበት፡፡ ከዚያ እያንዳንዱ ሰው ማጠኛውን በያዌ ፊት ያምጣ፣ ሁለት መቶ አምሳዎቹ ሰዎችህ ማጠኛዎቻቸውን ይዘው ይቅረቡ፡፡ አንተና አሮንም ደግሞ የየራሳቸችሁን ማጠኛ አምጡ፡፡” 18 ስለዚህ እያንዳንዱ ሰው ማጠኛውን ወሰደ፣ በውስጡ እሳት አደረገ፣ እጣንም ጨመረበት ከሙሴና ከአሮን ጋር በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ ቆሙ፡፡ 19 ቆሬ መላውን ማህበረሰብ በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ላይ በሙሴና በአሮን ላይ በተቃውሞ ሰበሰበ፣ የያህዌ ክብር ደግሞ ለማህበረሰቡ ሁሉ ታየ፡፡ 20 ከዚያ ያህዌ ለሙሴና ለአሮን እንዲህ ሲል ተናገረ፣ 21 ”በቶሎ ከማጠፋው ከዚህ ማህበረሰብ መሀል ራሳችሁን ለዩ፡፡” 22 ሙሴና አሮን በግንባራቸው ተደፍተው እንዲህ አሉ፣ “ የሰው ልጆች ሁሉ መንፈስ አምላክ የሆንክ እግዚአብሔር ሆይ፣ አንድ ሰው ኃጢአት ቢሰራ ማህበረሰቡን በሙሉ ልትቆጣ ይገባልን?” 23 ያህዌ ለሙሴ እንዲህ ሲል መለሰለት፣ 24 ”ለማህበረሰቡ እንዲህ በል፣ ‘ከቆሬ፣ ከዳታንና ከኤብሮን ድንኳኖች ውጡ፡፡’” 25 ከዚያ ሙሴ ተነስቶ ወደ ወደ ዳታንና አብሮን ሄደ፤ የእስራኤል መሪዎች እርሱን ተከተሉት፡፡ 26 ለማህበረሰቡ እንዲህ ብሎ ተናገረ፣ “አሁን የእነዚህን ክፉ ሰዎች ድንኳኖች ልቀቁ፣ የእነርሱ የሆነውን አንዳች ነገር አትንኩ፣ አለበለዚያ በእነርሱ ኃጢአቶች ሁሉ እናንተም ትጠፋላችሁ፡፡” 27 ስለዚህ በቆሬ፣ በዳታንና በኤብሮን ድንኳኖች በእያንዳንዱ አቅጣጫ የሚገኝ ማህበረሰብ ከእነርሱ ራቁ፡፡ ዳታንና አብሮን ወደ ውጭ ወጥተው ከሚስቶቻቸው፣ ከወንዶች ልጆቻቸውና ከህፃናቶቻቸው ጋር በድንኳኖቸው ደጃፍ ላይ ቆሙ፡፡ 28 ከዚያ ሙሴ እንዲህ አለ፣ “በዚህም ያህዌ እነዚህን ስራዎች ሁሉ እንድሰራ እንደላከኝ ታውቃላችሁ፣ እኔ በራሴ ፈቃድ እነዚህን ነገሮች አልሰራኋቸውም፡፡ 29 እነዚህ ሰዎች በተለመደው ሁኔታ ተፈጥሯዊ ሞት ቢሞቱ፣ ያህዌ እኔን አላኝም ማለት ነው፡፡ 30 ነገር ግን ያህዌ ምድሪቷን ቢከፍትና እርሷ እንደ ተከፈተ አፍ ሆና፣ ከነቤተሰቦቻቸው ብትውጣቸው፣ ደግሞም በህይወታቸው ሳሉ ወደ ሲኦል ቢወርዱ፣ ያን ጊዜ እነዚህ ሰዎች ያህዌን እንደናቁ ታውቃላችሁ፡፡” 31 ሙሴ እነዚህን ቃላቶች ተናግሮ እንደጨረሰ፣ ምድሪቱ ከነዚህ ሰዎች በታች ተከፈተች፡፡ 32 መሬት አፏን ከፈተችና ዋጠቻቸው፣ ቤተሰቦቻቸው፣ እና የቆሬ ሰዎች ሁሉ እንዲሁም ያላቸው ሀብት ሁሉ ተዋጠ፡፡ 33 እነርሱና በየቤተሰባቸው እያንዳንዱ በሕይወት ሳሉ ወደ ሲኦል ወረዱ፡፡ መሬት በላያቸው ተከደነች፣ እናም በዚህ መንገድ ከማህበረሰቡ መሀል ጠፉ፡፡ 34 በዙሪያቸው የነበሩ እስራኤላዊያን ሁሉ ከጩኸታቸው የተነሳ ሸሹ፡፡ እንዲህ እያሉም ጮኹ፣ “መሬት እኛንም ደግሞ ልትውጠን ነው!” 35 እሳት ከያህዌ ዘንድ ወጥታ የሚያጥኑትን 250 ሰዎች በላቻቸው፡፡ 36 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 37 ”ጥናዎቹ ለእኔ የተለዩ ናቸውና ለካህኑ ለአሮን ልጅ ለአላዓዛር ከሚጤሱት የተረፉትን ጥናዎች እንዲወስድ ንገረው፡፡ ከዚያ ረመጡን ይበትኑት፡፡ 38 በኃጠአታቸው ምክንያት ሕይወታቸውን ያጡትን ሰዎች ጥናዎች ውሰድ፡፡ ጥናዎቹ የተቀጠቀጡ ሰሀኖች ተደርገው ለመሰዊያው መሸፈኛነት ይዋሉ፡፡ ለእኔ የተለዩ ናቸውና፣ እነዚያ ሰዎች በእኔ ፊት ያቅርቧቸው፡፡ እነዚህም ለእስራኤል ሰዎች ለእኔ መገኘት ምልክት ይሆናሉ፡፡” 39 ካህኑ አልዓዛር የተቃጠሉት ሰዎች ይጠቀሙባቸው የነበሩትን የናስ ጥናዎች ይውሰድና ለመሰዊያው መሸፈኛነት ይቀጥቅጣቸው፣ 40 ይህም፤ ለእስራኤል ሰዎች ማስታወሻ እንዲሆን፣ ማንም የአሮን ትውልድ ያልሆነ መጻተኛ በያህዌ ፊት ለማጠን እንዳያቀርብና እንደ ቆሬና እንደ እርሱ ተከታዮች እንዳይሆኑ ያህዌ በሙሴ በኩል እንዳዘዘው ልክ እንደዚያ እንዳይሆንባቸው ነው፡፡ 41 ነገር ግን በማግስቱ የእስራኤል ማህበረሰብ በሙሉ በሙሴና በአሮን ላይ በማጉረምረም ተነሱባቸው፡፡ እነዲህም አሉ፣ “እናንተ የያህዌን ሰዎች ገድላችኋል፡፡” 42 ከዚያም እንዲህ ሆነ፣ ማህበረሰቡ በሙሴና በአሮን ላይ በተቃውሞ ሲሰበሰብ፣ ወደ መገናኛው ድንኳን አሻግሮ ሲመለከቱ፣ እነሆ ደመናው ድንኳኑን ሸፍኖት ነበር፡፡ የያህዌ ክብር ታየ፣ 43 እናም ሙሴና አሮን ወደ መገናኛው ድንኳን ወደፊት መጡ፡፡ 44 ከዚያ ያህዌ ሙሴን ተናገረው፡፡ እንደህም አለው፣ 45 “ከዚህ ማህበረሰብ ፊት ራቅ፣ እኔ በቶሎ አጠፋቸዋለሁ፡፡” ከዚያ ሙሴና አሮን በግምባራቸው ተደፉ፡፡ 46 ሙሴ አሮንን እንዲህ አለው፣ “ማጥንቱን ውሰድ፣ ከመሰዊያው እሳት ወስደህ አድርግበት፣ በውስጡ እጣን ጨምርበት፣ በቶሎ ወደ ማህበረሰቡ ውሰደው፣ እናም ለእነርሱ አስተሰርይ፣ ምክንያቱም ከያህዌ ዘንድ ቁጣ እየመጣ ነው፡፡ መቅሰፍቱ ጀምሯል፡፡” 47 ስለዚህም አሮን ሙሴ እንደመራው አደረገ፡፡ ወደ ማህበረሰቡ መሃል ሮጠ፡፡ መቅሰፍቱ በህዝቡ መካከል በፍጥነት መስፋፋት ጀመሮ ነበር፣ ስለዚህም እርሱ እጣኑን ጨምሮ ለህዝቡ ማስተሰርያ አደረገ፡፡ 48 አሮን በሙታኑና በህያዋኑ መሀል ቆመ፣ በዚህ መንገድ መቅሰፍቱ ቆመ፡፡ 49 በመቅሰፍቱ የሞቱት ሰዎች ቁጥር 14700 ነበር፣ ይህም በቆሬ ምክንያት የሞቱትን ሳይጨምር ነው፡፡ 50 አሮን ወደ መገናኛው ድንኳን መግቢያ ወደ ሙሴ ተመለሰ፣ መቅሰፍቱም አበቃ፡፡



Numbers 16:1

ቀአት

የዚህን ሰው ሥም በኦሪት ዘኁልቁ 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በሙሴ ላይ ተነሱ

በአንድ በኃላፊነት በሚገኝ ሰው ላይ ማመፅና መተቸት ልክ ለመጣላት እንደተነሱ ዓይነት ነገር ተደርጎ ተገልጿል፡፡“በሙሴ ላይ አመፁ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሁለት መቶ ሃምሣ

“250”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ታዋቂ የሆኑ የማህበረሰቡ አባላት

“ዝነኛ የሆኑ የማህበረሰቡ አባላት” ወይም“በማህበረሰቡ ውስጥ ዋና የሆኑ ሰዎች”

እናንተ እጅግ አብዝታችኋል

ይሄ የሚያመለከተው አንድ ሰው ማድረግ ከሚገባው በላይ ማድረጉን ነው፡፡“ማድረግ ከሚገባችሁ በላይ አድርጋችኋል”ወይም “ሊኖራችሁ ከሚገባው በላይ የሆነ ሥልጣን ያላችሁ ይመሰላችኋል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ጉባዔ ላይ ለምን ትታበያላችሁ?

ሰዎቹ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቁት ሙሴንና አሮንን ለመገሰፅ ብለው ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ “በተቀረው የእግዚአብሔር ጉባዔ ላይ ራሣችሁን ከፍ ማድረጋችሁ ትክክል አይደለም” (ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሌሎቹ በላይ ራሣችሁን ከፍ ማድረጋችሁ

አንድ ሰው አስፈላጊ ነኝ ብሎ የማመኑን ነገር ራስን ከፍ ከማድረግ ጋር ተነፃፅሯል፡፡“ራሣችሁን ከሌሎች የበለጠ አስፈላጊ ነን ብላችሁ ትገምታላችሁ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:4

በግምባሩ ወደቀ

ይሄ የሚያሣየው ሙሴ በእግዚአብሔር ፊት ራሱን ማዋረዱን ነው፡፡በእግዚአብሔርና በመረጣቸው ሰዎች ላይ በማመፃቸው እግዚአብሔር ሕዝቡን ሊቀጣ ይችላል ብሎ ፈራ፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት)

ለእርሱ የሚሆነውን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ለራሱ የለየውን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:6

ማያያዣ ዓረፍተ ነገሮች

ሙሴ ለቀአትና ከቀአት ጋር ለነበሩት ሰዎች መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ጥና

ዕጣንን ለማጤስ የሚያገለግል ዕቃ፡፡

በእግዚአብሔር ፊት

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“በእግዚአብሔር ሕልውና ፊት”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ያ ሰው ለእግዚአብሔር የተለየ ይሆናል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ያንን ሰው ለራሱ የተለየ ያደርገዋል” (ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እናንተ እጅግ አብዝታችኋል

ይሄ የሚያመለከተው አንድ ሰው ማድረግ ከሚገባው በላይ አልፎ ማድረጉን ነው፡፡“ማድረግ ከሚገባችሁ በላይ አድርጋችኋል”ወይም “ሊኖራችሁ ከሚገባው በላይ የሆነ ሥልጣን ያላችሁ ይመሰላችኋል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:8

አይበቃችሁምን..እነርሱን ለማገልገል

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የሚያነሣው ቀአትንና ከእርሱ ጋር የነበሩትን ሰዎች ለመገሰፅ ብሎ ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እነርሱን ማገልገል ትንሽ ነገር መስሎ ይታያቸኋል”ወይም “እነርሱን ማገልገል እንደ ትንሽ ነገር መስሎ ሊታያችሁ አይገባም፡፡”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእናንተ ትንሽ ነገር

“ለእናንተ የማይበቃችሁ” ወይም “ለእናንተ ጠቃሚ ያልሆነ”

ክህነትንም ትፈልጋላችሁ

ክህነት መፈለግን ልክ በዓይናቸው እንደሚፈልጉት ዓይነት በሚመስል መልኩ ተገልጿል፡፡“ክሀነትን ትፈልጋላችሁ” ወይም “እናንተም ካህናት መሆን ትፈልጋላችሁ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን በሚያገለግለው በአሮን ላይ ለምን ታጉረመረማላችሁ?

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የሚያነሳበት ምክኒያት የአሮንን መልካም የሆነ ድርጊት በመጥቀስ ለመሞገት ነበር፡፡ምክኒያቱ ደግሞ አሮን እግዚአብሔር አድርግ የሚለውን ነገር የሚያደረግ ሰው ሰለነበረ ነው፡፡“የምታጉመርሙት በአሮን ላይ ሣይሆን አሮንን በሚያዝዘው በእግዚአብሔር ላይ ነው”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:12

በምድረ በዳ ትገድለን ዘንድ …ያወጣኸን አይበቃህምን?

ዳታንና አቤሮን ይህንን ጥያቄ የሚጠይቁት ሙሴን ለመገሰፅ ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እኛን እዚህ ምድረ በዳ አምጥተህ በምድረ በዳ ልትገድለን ማሰብህን ምንም እንዳልሆነ ነገር ቆጥረኸዋል”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ትንሽ ነገር

“በቂ ያልሆነ”ወይም “ጠቃሚ ያልሆነ”

ወተትና ማር ወደምታፈስስ ምድር

ምድሪቱ ለከብቶችና ለዕፅዋት ተስማሚ መሆኗን ለመግለፅ ከእነዚያ እንስሳት የሚገኘው ወተትና ማር ልክ በምድሪቱ ላይ እንደሚፈስስ ነገር አድርገው ይገልፁታል፡፡ይህንን ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 14፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ከብቶችን ለማርባትና እህልን ለማብቀል እጅግ የያመች ሥፍራ ነው”ወይም “እጅግ ለም የሆነ መሬት ነው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ልትገድለን

ሰዎቹ ነገሩን አጋንነው የሚናገሩት ከአነርሱ ውስጥ አንድ ሰው ቢሞት ሙሴን ተጠያቂ ለማድረግ በማሰብ ነው፡፡(የተጋነነ ንፅፅር እና አጠቃላይነት የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ ርስት

እግዚአብሔር ለዘላለም የሚሰጣቸውን ነገር በውርስ እንደሚያገኙት ነገር አድርገው ነው የሚናገሩት፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በባዶ ተስፋ ዓይኖቻችንን ታሳውራለህን?

ሰዎቹ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቁት ሙሴን ለመቃወም ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በባዶ ተስፋ ልታሳውረን ትፈልጋለህ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ልታሳውረን

ሰዎችን ማታለል ሰዎችን እንደ ማሳወር ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ልታታልለን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በባዶ ተስፋ

ተስፋ የተሰጣቸው ነገሮች ያለመከናወናቸውን ለመግለፅ ባዶ ከሆነ ዕቃ ማስቀመጫ ጋር ያነፃፅሩታል፡፡“የማትፈፅማቸው የተስፋ ቃሎችህ”ወይም “እነዚህ ነገሮች ይደረጋሉ እያልክ የማታከናውናቸው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:15

ከእነርሱ አንድ አህያ ስንኳ አልወሰድኩም

እዚህ ላይ አንድ “አህያ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው አንድ ሰው ከሌላ ሰው ሊወስድ የሚችለውን ነገር ነው፡፡“ከእነርሱ አንዲት ነገር አልወሰድኩም፡፡አንድ አህያ እንኳን”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

ጥና

ዕጣንን ለማጤስ የሚያገለግል ዕቃ፡፡

Numbers 16:20

አጠፋቸው ዘንድ

እነርሱን ማጥፋት ልክ እግዚአብሔር እንደሚበላቸው ዓይነት ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡“አጠፋቸው ዘንድ”ወይም “አጠፋቸዋለሁ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በግምባር መውደቅ

ይሄ የሚያሣየው ሙሴና አሮን በእግዚአብሔር ፊት ራሣቸውን ማዋረዳቸውን ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

የሰው ሁሉ ነፍስ አምላክ

እዚህ ላይ “ነፍስ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ለመኖር ብቁ መሆንን ነው፡፡“ለሰው ሁሉ ሕይወትን የሚሰጠው እግዚአብሔር” (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

አንድ ሰው ኃጢአት ቢሰራ በማህበሩ ሁሉ ትቆጣለህን?

ሙሴና አሮን ይህን ጥያቄ የሚጠይቁት ስለ ሕዝቡ ልመናን ለማቅረብ ብለው ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንድ ሰው ኃጢአትን በመሥራቱ እባክህን በማህበሩ ሁሉ ላይ አትቆጣ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:25

ትጠፋላችሁ

መጥፋታቸው ልክ አንደ ምግብ እንደሚበሉ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ትጠፋላችሁ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በኃጢአታቸውም ትጠፋላችሁ

ከኃጢአታቸው የተነሣ መጥፋታቸው ልክ ኃጢአት እንደሚያጠፋቸው ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“በኃጢአታቸውም ትጠፋላችሁ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በኃጢአታቸውም ትጠፋላችሁ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የሰራችኋቸው ኃጢአቶቻችሁ ሁሉ ያጠፏችኋል”ወይም “ከኃጢአቶቸቻው ሁሉ የተነሣ እግዚአብሔር ያጠፋችኋል” (ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:28

በዚህ ታውቃላችሁ

እዚህ ላይ “በዚህ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴ ቀጥሎ የሚናገረውን ነገር በሚመለከት ነው፡፡

ምድር አፍዋን ከፍታ ትውጣቸዋለች

ሙሴ እዚህ ላይ የሚናገረው ልክ ምድር ሕይወት እንዳለው ነገር ሆኖ እነዚህ ሰዎች የሚወድቁበት የተከፈተ ጉድጓድ ደግሞ ሊበላቸው እንደተዘጋጀ ሠፊ አፍ አስመስሎ ነው፡፡“ከበታቻቸው ያለው መሬት ተሰነጠቀ፤ምድርም አፍዋን ከፍታ ዋጠቻቸው”(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:31

ምድርም አፍዋን ከፍታ ዋጠቻቸው

ሙሴ እዚህ ላይ የሚናገረው ልክ ምድር ሕይወት እንዳለው ነገር ሆኖ እነዚህ ሰዎች የሚወድቁበት የተከፈተው ጉድጓድ ደግሞ የምድርን አፍ አስመስሎ ነው፡፡“ከበታቻቸው ያለው መሬት እንደ ሠፊ አፍ ተከፍቶ በዚያ ወደቁና በእርሱ ውስጥ ተቀበሩ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:33

ወደ ሲኦል ወረዱ

በኦሪት ዘኁልቁ 16፡30 ላይ ተመሳሳይ የሆነ ሐረግ ይገኛል፡፡እዚያ ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

እነርሱ ተደነቁ

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው “እሥራኤላውያንን ሁሉ”ነው፡፡

ምድሪቱ እኛንም እንዳትውጠን

ሰዎቹ የሚናገሩት ልክ ምድር ሕይወት እንዳላት ነገር አድርገው ነው፡፡“ምናልባት መሬት ተከፍታ እኛንም ልትውጠን ትችላለች”ወይም “ምድር እንደገና የምትከፈት ከሆነ እኛም እዚያ ውስጥ ወድቀን ልንቀበር እንችላለን” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እሳትም ከእግዚአብሔር ዘንድ ወጥታ ሁለት መቶ ሃምሳ ሰዎች በላች

በእሣት መጥፋታቸው ልክ በእሣት እንደተበሉ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡ “እሳትም ከእግዚአብሔር ዘንድ ወጥቶ 250 ሰዎች አጠፋ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

250 ሰዎች

“ሁለት መቶ ሃምሳ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:36

ከእሳቱ ውስጥ

ይሄ 250 ሰዎች ያቃጠለውን እሳት የሚያመለክት ነው፡፡

ሕይወታቸውን ያጡት ሰዎች

ሕይወት ማጣት የሚያመለክተው መሞታቸውን ነው፡፡“የሞቱት ሰዎች”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱ የተሰሩ ይሁኑ

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ጥናዎቹን ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ “ካህኑ አልዓዛር ይጠፍጥፋቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱ የተቀደሱ ናቸው…እነርሱ ምልክት ይሆናሉ

“እነርሱ”እና“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ጥናዎቹን ነው፡፡

Numbers 16:39

የተቃጠሉት ሰዎች ያቀረቧቸውን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የተቀቃጠሉት ሰዎች የተጠቀሙባቸውን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በቆሬና በወገኑ

እንደ እነርሱ እንዴት ሊሆኑ እንደሚችሉ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ቆሬና ወገኑ እንደሞቱ መሞት”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:41

እንዲህም ሆነ

ይሄ ሐረግ ጥቅም ላይ እንዲውል የተደረገው በታሪኩ ውስጥ ጠቃሚ ክስተት መኖሩን ለማመልከት ነው፡፡

በሙሴና በአሮን ላይ አጉረመረሙ

“በሙሴና በአሮን ላይ ለማጉረምረም ተሰባሰቡ”

እነሆም ከደመናው

“በድንገት ደመናው” እዚህ ላይ“እነሆም”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በተመለከቱት ነገር ሰዎቹ መደነቃቸውን ነው፡፡

Numbers 16:44

አጠፋቸው ዘንድ

እግዚአብሔር እነርሱን የማጥፋቱን ነገር እንደሚበላቸው ዓይነት ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡“አጠፋቸው ዘንድ”ወይም “አጠፋቸዋለሁ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በግምባራቸው ወደቁ

ይሄ የሚያመለክተው ሙሴና አሮን በእግዚአብሔር ፊት ራሣቸውን ማዋረዳቸውን ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

ከእግዚአብሔር ፊት ቁጣ ወጥቶአልና

ቁጣ ከእግዚአብሔር ዘንደ ወጥቶአል የሚለው ቃል የሚያሣየው እግዚአብሔር መቆጣቱን ነው፡፡“እግዚአብሔር መቆጣቱን እያሳየ ነው” ወይም “እግዚአብሔር በጣም ከመቆጣቱ የተነሣ ቁጣውን ወደ ተግባር እየለወጠው ነው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:47

ዕጣንም ጨመረ

ዕጣኑን በጥናው ላይ ማድረጉ የሚያመለክተው ማቃጠሉን ነው፡፡“ዕጣኑን አቃጠለው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

መቅሰፍቱም ተከለከለ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“መቅሠፍቱ መስፋፋቱን አቆመ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 16:49

በቁጥር 14,700

“በቁጥር አሥራ አራት ሺህ ሰባት መቶ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 17

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 ”ለእስራኤል ሰዎች ተናገራቸው፡፡ ከእነርሱ በትሮችን ውሰድ፣ ከየነገዱ አባቶች አንድ በትር ውሰድ፡፡ ከእያንዱ መሪ አንድ በአጠቃላይ ከየነገድ የተመረጡ አስራ ሁለት በትሮችን ውሰድ፡፡ የእያንዳንዱን ሰው ስም በበትሩ ላይ ጻፍ፡፡ 3 የአሮንን ስም በሌዊ በትር ላይ ጻፍ፡፡ ለእያንዳንዱ መሪ ከየአባቶቹ ነገድ አንድ በትር ሊኖር ያስፈልጋል፡፡ 4 በትሮቹን ከአንተ ጋር በምገናኝበት በመገናኛው ድንኳን ከምስክሩ ኪዳን ፊት አስቀምጣቸው፡፡ 5 እንዲህ ይሆናል፣ እኔ የምመርጠው ሰው በትር ታቆጠቁጣለች፡፡ የእስራኤለ ሰዎች በአንተ ላይ የሚያደርጉትን ማጉረምረማቸውን እንዲያቆሙ አደርጋለሁ፡፡” 6 ሙሴ ለእስራኤል ሰዎች ተናገረ፡፡ ሁሉም የነገዱ መሪዎች በትሮቻቸውን ሰጡት፣ ከእያንዳንዱ መሪ አንድ በትር፣ ከየነገዱ አባቶች ተመረጠ፣ በአጠቃላይ አስራ ሁለት በትሮች ተመረጡ፡፡ የአሮን በትር ከእነዚህ መሀል ነበር፡፡ 7 ከዚያ ሙሴ እነዚህን በትሮች ወስዶ በያህዌ ፊት በምስክሩ ድንኳን ውስጥ አስቀመጣቸው፡፡ 8 በማግስቱ ሙሴ ወደ ምስክሩ ድንኳን ሄደ፣ እናም የሌዊ ነገድ የሆነችው የአሮን በትር አቆጥቁጣ አየ፡፡ እምቡጥ አብቅላ፣ አበባና ለውዝም አፍርታ ነበር! 9 ሙሴ በትሮቹን ሁሉ ከያህዌ ፊት ወደ እስራኤል ሰዎች ሁሉ አመጣቸው፡፡ እያንዳንዱ ሰው የራሱን በትር አግኝቶ ወሰደ፡፡ 10 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “የአሮንን በትር በምስክሩ ፊት አስቀምጣት፡፡ ባመፁት ሰዎች ላይ ለበደላቸው ምልክት ይሆን ዘንድ አስቀምጣት፣ ስለዚህም በእኔ ላይ የሚያሰሙትን ማጉረምረም ፍጻሜ ታደርግለታለህ፤ ይህ ካልሆነ ይሞታሉ፡፡” 11 ሙሴ ልክ ያህዌ እንዳዘዘው አደረገ፡፡ 12 የእስራኤል ሰዎች ሙሴን፣ “እኛ ሁላችንም እዚህ መሞታችን ነው፣ ሁላችንም መጥፋታችን ነው! 13 ወደ ያህዌ ማደሪያ ድንኳን የቀረቡ፣ እያንዳንዳቸው ወደዚህ የመጡ ይሞታሉ፡፡ ሁላችንም መጥፋት ይኖርብናልን?” አሉት፡፡



Numbers 17:1

አሥራ ሁለት

“12” (ቁጥሮች የሚለውን ይመለክቱ)

Numbers 17:3

የዓረፍተ ነገር ማያያዣ

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

የሌዊ ነገድ

እዚህ ላይ ሌዊ የሚለው ቃል የሚያመለክተው የሌዊን ነገድ ነው፡፡

ለአባቶቻቸው ቤቶች አለቃ

እዚህ ላይ “አለቃ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው “እያንዳንዱን”መሪ ነው፡፡

የምሥክሩ ድንኳን

“የምሥክሩ ድንኳን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ምሥክሩየተፃፉበት ሠሌዳ የሚቀመጥበትን ሣጥን ነው፡፡“የምሥክሩ ድንኳን”ወይም “ምሥክሩን የሚይዘው ሣጥን”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

የመረጥኩት ሰው በትር ታቆጠቁጣለች

“በመረጥኩት ሰው በትር ላይ የለመለመ ነገር ይወጣል”

በአንተ ላይ የሚናገሩትን የእሥራኤልን ልጆች ማጉረምረም አስቁም

እዚህ ላይ “ማጉረምረም”የሚለው አሕፅሮተ ሥም ሲሆን በግሥ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ “የእሥራኤል ሕዝብ በአንተ ላይ ከማጉረምረም እንዲታቀቡ አድርጋቸው”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 17:6

እያንዳንዱ አለቃ ከየአባቶቹ ቤት የተመረጠ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ከእያንዳንዱ ነገድ ሙሴ የመረጠው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የምሥክሩ ድንኳን

“የምሥክሩ ድንኳን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ምሥክሩ የተፃፉበት ሠሌዳ የሚቀመጥበትን ሣጥን ነው፡፡“የምሥክሩ ድንኳን”ወይም “ምሥክሩን የሚይዘው ሣጥን”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 17:8

እንዲህም ሆነ

“እንዲህም ሆነ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አንድ ልዩ የሆነ ነገር መከናወኑን ነው፡፡በእናንተ ቋንቋ ተመሳሳይ የሆነ አገላለፅሊኖራችሁ ይችል ይሆናል፡፡

Numbers 17:10

የምሥክሩ ድንኳን

“የምሥክሩ ድንኳን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ምሥክሩ የተፃፉበት ሠሌዳ የሚቀመጥበትን ሣጥን ነው፡፡“የምሥክሩ ድንኳን”ወይም “ምሥክሩን የሚይዘው ሣጥን”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

በአንተ ላይ የሚናገሩትን የእሥራኤልን ልጆች ማጉረምረም አስቁም

እዚህ ላይ “ማጉረምረም”የሚለው አሕፅሮተ ሥም ሲሆን በግሥ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ “የእሥራኤል ሕዝብ በአንተ ላይ ከማጉረምረም እንዲታቀቡ አድርጋቸው”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

አለበለዚያ ይሞታሉ

በማጉረምረማቸው የሚቀጥሉ ከሆነ የሚከሰተው ነገር ይሄ ነው፡፡እግዚአብሔር ይሄ እንዳይሆን ነበር የሚሻው፡፡“እንዳይሞቱ”(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 17:12

እንሞታለን፤ሁላችን እንጠፋለን

በመሠረቱ እነዚህ ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ተቀናጅተው የቀረቡበት ምክኒያት ለጉዳዩ አፅንኦት ለመስጠት ተፈልጎ ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 18

1 “ያህዌ አሮንን እንዲህ አለው፣ “አንተ፣ ወንዶች ልጆችህና የአባትህ ቤቶች በቤተ መቅደሱ ላይ ለሚሰራው በደል ተጠያቂ ትሆናላች፡፡ በክህነቱ ላይ ለሚፈፀሙ በደሎች ሁሉ ግን አንተና ከአንተ ጋር ያሉ ወንዶች ልጆች ብቻ ተጠያቂ ትሆናላችሁ፡፡ 2 ከአባትህ ነገድ የሆኑት ሌዋዊያንን በሚመለከት ከአንተ ጋር ይሆኑና አንተና ልጆችህ በምስክሩ ድንኳን ፊት ስታገለግሉ እንዲረዷችሁ አምጣቸው፡፡ 3 እነርሱ አንተንና መላውን ድንኳን ያገልግሉ፡፡ ሆኖም፣ ወደ ተቀደሰው ስፍራ ማናቸውም ነገሮች አይቅረቡ ወይም ከመሰዊያው ጋር አይነካኩ፣ አለበለዚያ እነርሱና አንተም ጭምር ትሞታላችሁ፡፡ 4 እነርሱ ከአንተ ጋር ሆነው ለመገናኛው ድንኳንና ከድንኳኑ ጋር ለተያያዙ ስራዎች ሁሉ እንክብካቤ ማድረግ አለባቸው፡፡ መጻተኛው ወደ አንተ አይጠጋ፡፡ 5 አንተ ለተቀደሰው ስፍራና ለመሰዊያው ሀላፊነት መውሰድ አለብህ፣ እንደገና ቁጣዬ በእስራኤል ሰዎች ላይ እንዳይመጣ ይህን አድርግ፡፡ 6 ከእስራኤል ትውልዶች መሀል ሌዋውያንን የመረጥኩት እኔ ራሴ ነኝ፡፡ እነርሱ ከመገናኛው ድንኳን ጋር የተያያዙ ሥራዎችን ለመስራት ለእኔ የተሰጡ ለእናንተ ስጦታዎች ናቸው፡፡ 7 ከመሰዊያውና በመጋረጃው ውስጥ ያሉትን አገልግሎቶች ሁሉ በሚመለከት ግን የክህነቱን ስራ የምትሰሩት አንተና ወንዶች ልጆችህ ብቻ ናችሁ፡፡ አንተ ራስህ እነዚያን ሀላፊነቶች መወጣት አለብህ፡፡ እኔ ክህነቱን ስጦታ አድርጌ ሰጥቼሃለሁ፡፡ ማናቸውም መጻተኛ ወደዚህ ቢጠጋ ይገደል፡፡” 8 ከዚያ ያህዌ አሮንን እንዲህ አለው፣ “ለእኔ የሚወዘወዙትን መስዋዕቶችና የእስራኤል ሰዎች ለእኔ የሰጧቸውን ቅዱስ መስዋዕቶች አያያዝ ሀላፊነቶች ሰጥቼሃለሁ፡፡ እነዚህን ስጦታዎች ቀጣይ ድርሻህ አድርጌ ለአንተና ለወንዶች ልጆችህ ሰጥቻለሁ፡፡ 9 ለያህዌ ሙሉ ለሙሉ ከተለዩ ከእነዚህ ስጦታዎች ውስጥ ሙሉ ለሙሉ የማይቃጠሉት የአንተ ናቸው፡፡ ህዝቡ የሚያመጣው ማናቸውም መስዋዕት፣ የእህል ቁርባኑን፣ የኃጢአት መስዋዕቱን፣ እና የበደል መስዋዕቱን ሁሉ ጨምሮ፣ እነዚህ እጅግ ቅዱስ የሆኑ ለእኔ የሚለይዋቸውና የሚያመጧቸው ስጦታዎች የአንተና የወንዶች ልጆችህ ይሆናሉ፡፡ 10 አንተ የምትመገባቸው እነዚህ ስጦታዎች፣ ሙሉ ለሙሉ ለእኔ የተለዩ ናቸው፡፡ በመሀል የሚገኝ ማናቸውም ወንድ እነዚህን ስጦዎች ይብላ፡፡ እነርሱ በእናንተ ዘንድ ለእኔ የተለዩ ተደርገው ይቆጠሩ፡፡ 11 እነዚህ የእናንተ ስጦታዎች ናቸው፡፡ ከእስራኤል ሰዎች ከሚሰበሰቡ መስዋዕቶች ውስጥ የተለዩት ስጦታዎቻቸው ሁሉ፣ በእኔ ፊት የተወዘወዙና ለእኔ የቀረቡ ስጦዎች ሁሉ የእናንተ ናቸው፡፡ እነዚህን ለእናንተ፣ ለወንዶች ልጆቻችሁ፣ እና ለሴቶች ልጆቻችሁ፣ ቀጣይ ድርሻችሁ አድርጌ ሰጥቻለሁ፡፡ እያንዳንዱ በቤተሰብህ ውስጥ የመንጻት ሥርዓት የፈፀመ ሁሉ ከእነዚህ ስጦታዎች መመገብ ይቻላል፡፡ 12 ከዘይቱ ምርጥ የሆነውን፣ ከአዲሱ ወይንና ሰብል ምርጡን፣ ህዝቡ ለእኔ ካቀረበው በኩራቱን፣ እነዚህን ሁሉ ለእናንተ ሰጥቻለሁ፡፡ 13 ለእኔ የሚያመጡት፣ በምድራቸው ካለው በመጀመሪያ የደረሰው ፍሬ ሁሉ የአንተ ነው፡፡ በቤተሰብህ ውስጥ ያለ ንጹህ የሆነ ሁሉ እነዚህን ነገሮች መብላት ይችላል፡፡ 14 በእስራኤል ማናቸው ፈጽሞ የተሰጠ ነገር የአንተ ይሆናል፡፡ 15 እያንዳንዱ ማህጸን የሚከፍት ሁሉ፣ ሰዎች ለያህዌ የሰጡት በኩር ሁሉ፣ የሰውም ይሁን የእንስሳ በኩር የአንተ ይሆናል፡፡ የሆነ ሆኖ፣ ሰዎቹ መጀመሪያ የተወለደውን ሁሉ መልሰው ይግዙ፣ ንጹህ ያልሆኑ እንስሳትን በኩራት መልሰው ይግዙ፡፡ 16 በሰዎች ተመልሰው የሚገዙ አንድ ወር ከሞላቸው በኋላ መልሰው ይገዙ፡፡ ከዚያ ሰዎቹ በመቅደሱ ሰቅል ዋጋ መልሰው ከሀያ ጌራ ጋር እኩል ዋጋ ባለው በአምስት ሰቅሎች ዋጋ ሊገዟቸው ይችላሉ፡፡ 17 ነገር ግን የላም በኩር፣ ወይም የበግ በኩር፣ ወይም የፍየል በኩር ከሆነ እነዚህን እንስሳት መልሰህ አትግዛ፤ እነዚህ ለእኔ የተሰዉ ናቸው፡፡ ለእኔ ጣፋጭ መዓዛ ለማቅረብ፣ ደማቸውን በመሰዊያ ላይ እርጨው፣ ስባቸውን በእሳት የቀረበ መስዋዕት አድርገህ ኣቃጥለው፡፡ 18 ስጋቸው ለአንተ ይሁን፡፡ ልክ እንደ ሚወዘወዘው ፍርምባና እንደ ቀኙ ወርች ስጋቸው የአንተ ይሆናል፡፡ 19 የእስራኤል ሰዎች ለእኔ ያቀረቧቸውን ቅዱስ የሆኑ መስዋዕቶች ሁሉ እኔ፤ ለአንተ፣ ለወንድ ልጆችህ እና ለሴት ልጆችህ ቀጣይ ድርሻ አድርጌ ሰጥቻችኋለሁ፡፡ ለጨው ኪዳንና ለዘለዓም የአንድነት መስዋዕት ሆነው በፊቴ ከአንተና ከትውልድህ ጋር ይኖራሉ፡፡” 20 ያህዌ አሮንን እንዲህ አለው፣ “አንተ በህዝቡ ምድር ርስት አይኖርህም፣ ወይንም ደግሞ በህዝቡ መሀል የሀብት ድርሻ አይኖርህም፡፡ በእስራኤል ህዝብ መሀል እኔ ድርሻህና ርስትህ ነኝ፡፡ 21 እስራኤላዊያን የሚያመጡትን አስራት ሁሉ፣ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ለሚሰጡት አገልግሎት ድርሻቸው አድርጌ ለሌዊ ትውልድ ሰጥቻቸዋለሁ፡፡ 22 ከአሁን አንስቶ ከእስራኤል ህዝቡ ወደ መገናኛው ድንኳን አይቅረብ፣ ከቀረቡ በኃጢአታቸው ሀላፊነትን ይወስዳሉ፤ እናም ይሞታሉ፡፡ 23 ከመገናኛው ድንኳን ጋር የተያያዙ ሥራዎችን ሌዋውያን ይስሩ፡፡ ይህን በሚመለከት ለማናቸውም ኃጢአት ተጠያቂ ይሆናሉ፡፡ ይህ በእናተ ህዝብ ትውልዶች ሁሉ ቀዋሚ ህግ ይሆናል፡፡ በእስራኤል ህዝብ መሀል ሌዋውያን ርስት ሊኖቸው አይገባም፡፡ 24 እስራኤላዊያን መባ አድርገው ለእኔ ያቀረቡትን አስራት እኔ ለሌዋውያን ርስታቸው አድርጌ የሰጠሁት እነዚህን ነው፡፡ ለዚህም ነው እንዲህ የምላቸው፣ ‘እነርሱ በእስራኤል ህዝብ መሀል ርስት አይኖራቸውም፡፡’” 25 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 26 ”ለሌዋውያን እንዲህ በላቸው፣ ‘ከእነርሱ የአንተ ርስት አድርጎ ያህዌ ለእናንተ የሰጣችሁን አስራት ከእስራኤል ሰዎች ስትቀበሉ፣ ከዚያ አስራት ለእርሱ አንድ አስረኛውን መባ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ፡፡ 27 እናንተ የምታቀርቡት መስዋዕት በእናንተ ዘንድ ከአውድማ እንደ ቀረበ የእህል አስራት ወይም ከወይን መጥመቂያ እንደ ቀረበ አስራት ሊቆጠር ይገባዋል፡፡ 28 እንደዚሁም ከእስራኤል ሰዎች ከተቀበላችሁት አስራት ሁሉ ለያህዌ መባ ማቅረብ አለባችሁ፡፡ ከእነዚህም ለካህኑ ለአሮን ለእግዚአብሔር ከቀረበው ስጦታ መስጠት አለባች፡፡ 29 ከተቀበላችሁት ስጦታ ሁሉ፣ ከእያንዳንዱ ለያህዌ መባ መስጠት አለባችሁ፡፡ ይህንን ምርጥ ከሆነው ሁሉና ለእናንተ ከሰጠኋችሁ እጅግ ከተቀደሱት ነገሮች ማድረግ አለባችሁ፡፡’ 30 ስለዚህም እንደዚህ በላቸው፣ ‘ከተቀበላችሁት ምርጡን ስታቀርቡ፣ ይህ በሌዋውያን ዘንድ ከአውድማ እንደቀረበ ምርትና ከወይን መጥመቂያ እንደቀረበ ሊቆጠር ይገባል፡፡ 31 የተቀረውን ስጦታዎቻችሁን በማንኛውም ስፍራ ልትበሉ ትችላላችሁ፣ እናንተና ቤተሰቦቻችሁ ብሉት፣ ምክንያቱም በመገናኛው ድንኳን ለምትሰጡት አገልግሎት ክፍያችሁ ነው፡፡ 32 ከተቀበላችሁት ምርጥ የሆነውን ለያህዌ ካቀረባችሁ፣ ያን በመብላታችሁና በመጠጣታችሁ ምንም አይት በደል በራሳችሁ ላይ አታመጡም፡፡ ነገር ግን የተቀደሱ የእስራኤል ህዝቦች ስጦታዎች አታቃሉ፣ አሊያ ትሞታላች፡፡



Numbers 18:1

በመቅደሱ ላይ የተሰራ ኃጢአት ሁሉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ማንኛውም ሰው በመቅደሱ ላይ የሚሰራው ኃጢአት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በማንኛውም ሰው በክህነት አገልግሎቱ ላይ የሚሰሩ ኃጢአቶች ሁሉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ማንኛውም ሰው በክህነት አገልግሎቱ ላይ የሚሰራው ኃጢአት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በክህነት አገልግሎት ውስጥ የሚገኝ ማንኛውም ሰው

“ማንኛውም ካህን”

Numbers 18:3

የዓረፍተ ነገር ማያያዣ

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል፡፡

አንተን ማገልገል ይኖርባቸዋል..እነርሱበአንድነት ይሁኑ

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሌዊ ነገድ አባላትን የሚያመለክት ሲሆን “አንተ”የሚለው ቃል ደግሞ የሚያመለክተው አሮንን ነው፡፡(አንተ/እናንተ የሚለው ቃል በተለያየ መንገድ የሚገለፅበት የሚለውን ይመልከቱ)

ወይም አንተና እነርሱ ትሞታላችሁ

እዚሀ ላይ “እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው“በቤተመቅደሱ ውስጥ ባሉት ሥፍራዎች ሁሉ”የመግባት መብት ያላቸውን ማንኛውንም የሌዊ ነገድ አባላትን ነው፡፡“እነርሱ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር ሲሆን የሚያመለክተውም አሮንንና በተፈቀደላቸው አገልግሎት ውስጥ የሚገኙትን ሌዋውያንን ነው፡፡“(ተውላጠ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ሌላ ሰው ወደ እናንተ አይቅረብ፡፡ኃላፊነቱን መውሰድ ይኖርባችኋል፡፡

እዚህ ላይ “እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር በመሆኑ የሚያመለክተው አሮንንና የተቀሩትን ሌዋውያን ነው፡፡(አንተ/እናንተ የሚለው ቃል በተለያየ መንገድ የሚገለፅበት የሚለውን ይመልከቱ)

ቁጣዬ በእሥራኤል ልጆች ላይ እንደገና እንዳይነድባቸው

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ እጅግ እንደተቆጣ ያመለክታል፡፡2/“በእሥራኤል ሕዝብ ላይ ዳግም በእጅጉ እንዳልቆጣ”2/ይሄ የሚያሣየው ከመቆጣቱ የተነሣ መቅጣቱን ያመለክታል፡፡“የእሥራኤልን ሕዝብ ደግሜ እንዳልቀጣ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:6

የዓረፍተ ነገር ማያያዣ

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ለእናንተ ሥጦታ ናቸው

እግዚአብሔር ሌዋውያን አሮንን እንዲያግዙት የመደበበትን ሁኔታ እግዚአብሔር ለአሮን እንደተሰጠ ሥጦታ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ለአንተ እንደ ሥጦታ ናቸው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ለእኔ የተሰጡ

ለእግዚአብሔር “የተሰጡ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ለማገልገል መለየታቸውን ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለራሴ የለየኋቸውን”ወይም“ለራሴ ለይቼያቸዋለሁ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውንና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አንተና የአንተ ልጆችህ ብቻ

እዚህ ላይ“አንተ”እና “የአንተ”የሚሉት ቃላት የነጠላ ቁጥር በመሆናቸው የሚያመለክቱት አሮንን ነው፡፡በሌሎች ሥፍራዎች ላይ “እናንተ”እና“የእናንተ”የሚሉት የብዙ ቁጥር በመሆናቸው የሚያመለክቱት አሮንንና ልጆቹን ነው፡፡(አንተ/እናንተ የሚለው ቃል በተለያየ መንገድ የሚገለፅበት የሚለውን ይመልከቱ)

ክህነታችሁን ጠብቁ

“የካህናትን ተግባር አከናውኑ”

በመጋረጃው ውስጥ ያለውን ሁሉ

በመጋረጃው ውስጥ የሚለው ቃል የሚያመለክተው ከመጋረጃው ጀርባ የሚገኘውን የውስጥ ክፍል ነው፡፡“ከመጋረጃው ጀርባ ባለው ከፍል ውስጥ የሚገኘውን ነገር ሁሉ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

እንግዳ የሆነ ሰው ቢቀርብ ይገደል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሌላ ሰው ቢቀርብ መገደል ይኖርበታል”ወይም “ሌላ ሰው ከቀረበ መግደል ይኖርባችኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ቢቀርብ

ሊቀርቡት የማይገባቸው ነገር ምን እንደሆነ በግልፅ ሊብራራ ይችላል፡፡“ቅዱሱን ሥፍራ የሚቀርብ ሰው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:8

ለእኔ የቀረበው የማንሣት ቁርባን

እዚህ ላይ “ማንሳት”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አንድን ነገር ለእግዚአብሔር መሥጠትን ወይም ማቅረብን ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰዎች ለእኔ የሚያቀርቧቸውመሥዋዕቶች”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እነዚህን የማንሣት ቁርባኖች ለአንተ ሰጥቼሃለሁ

እግዚአብሔር ይህንን ውሳኔ ቀድሞ የወሰነ በመሆኑ ጉዳዩን እንደፈፀመው ዓይነት አድርጎ ይናገራል፡፡“እነዚህን የማንሣት ቁርባኖች ለአንተ ሰጥቼሃለሁ”

ለልጆችህ ድርሻ እንዲሆን

ድርሻ ማለት አንድ ሰው የተወሰነውን የአንድ ነገር ክፍል ሲወስድ ማለት ነው፡፡“በማይቋረጥ መልኩ የምትወስዱት ድርሻችሁ”

ከእሣቱ ከተረፈው

“በመሠዊያው ላይ ሙሉ በሙሉ የማታቃጥሉት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:10

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል

Numbers 18:12

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል

የፍሬ መጀመሪያ

ይሄ የሚያመለክተው ጥራት ያላቸውንና የሚያመርቷቸውን ዘይት፤ወይንና እህልን ነው፡፡

በቤትህ ንፁሕ የሆነ ሁሉ

በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ማግኘትን ንፁሕ እንደመሆን አድርጎ አቅርቦታል፡፡“በቤትህ ውስጥ በእኔ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ሰው ሁሉ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:14

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል

ማሕፀንን የሚከፍት ሁሉ፤በኩራት የሆነ ሁሉ

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡“ማሕፀንን የሚከፍት ወንድ ሁሉ”(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ማሕፀንን የሚከፍት ሁሉ

“ማሕፀን መክፈት”የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገርእናት የምትወለደው የመጀመሪያ ወንድ ልጇ ማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በመጀመሪያ የተወለደውን ሁሉ ሰዎቸ ሊቤዡት ይገባል

መጀመሪያ የተወለደውን ወንድ ልጃቸውን መሥዋዕት ከማድረግ ይልቅ ለልጆቻቸው ሲሉ ለካህኑ ገንዘብ መክፈል ነበረባቸው፡፡

ሰዎች ከተተቤዧቸው ከአንድ ወር በኋላ ተመልሰው ሊቤዡ ይገባል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንድ ወር ከሞላቸው በኋላ ሰዎች መልሰው ሊቤዧቸው ይገባል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ዳግም ሊቤዡ የሚገባቸው ነገሮች

ይሄ ምናልባት የሚያመለከተው ሰዎችን እንጂ ንፁሕ ያልሆኑ እንስሳትን ለማመልከት አይመስልም፡፡

አምስት ሰቅል …ሃያ አቦሊ

በዘመናዊ የመለኪያ መንገድ መተቀም አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ እነዚሀን ተግባራዊ የማድረጊያ መንገዶች እነሆ፡፡“አምስት ብር ቁርጥራጮች….እያንዳንዱ አምስት ግራም ያህል የሚመዝን”ወይም“በቤተመቅደሱ ውስጥ ጥቅም ላይ ባሉት የጥራት ደረጃዎች መሠረት የሚመዝን አምሳ ግራም ብር”(መፅሐፍ ቅዱሣዊመለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

አምስት ሰቅል

ሰቅል የክብደት መለኪያ ነው፡፡የሚመዘነው ነገር ምን እንደሆነ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የቤተመቅደስሰቅል

የተለያየ ዓይነት የሰቅል ዓይነቶች ነበሩ፡፡ይሄኛው በመገናኛ ድንኳኑ ውስጥ በሚገኘው የተቀደሰው ሥፍራ ላይ ሰዎች የሚጠቀሙበት ዓይነት ነበር፡፡ሃያ አቦሊ ይመዝን ነበር፡፡ይሄ 11 ግራም ገደማ ይሆናል፡፡(መፅሐፍ ቅዱሣዊ መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:17

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ደማቸውን መርጨት ይኖርብሃል

በመጀመሪያ እንስሣቱን መግደል በተመለከተየበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“እንስሳቱን ገድለህ ደማቸውን ልትረጭ ይገባሃል” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሣት የተቃጠለ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእሣት የምትሰራውን”ወይም“በመሠዊያው ላይ በእሣት የምታቃጥለውን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ እንዲሆን

እግዚአብሔር በጣፋጭ ሽታ መደሰቱ የሚያመለክተው ቁርባኑን በሚሰዋው ሰው ደስ መሰኘቱን ነው፡፡“እና እግዚአብሔር በአንተ ደስ ይለዋል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ መወዘወወዝ ፍርምባ እንደ ቀኙም ወርች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የመወዝወዝ ፍርምባውንና ቀኙን ወርች እንደ መሥዋዕት የምታቀርቡልኝ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:19

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ለአንተ ሰጥቼሃለሁ

እግዚአብሔር ይህንን ውሳኔ ቀድሞ የወሰነ በመሆኑ ጉዳዩን እንደፈፀመው ዓይነት አድርጎ ይናገራል፡፡“ለአንተ ሰጠሁህ”

ለልጆችህ እንደሚቀጥል ድርሻ

ድርሻ ማለት አንድ ሰው የተወሰነውን የአንድ ነገር ክፍል ሲወስድ ማለት ነው፡፡“በማይቋረጥ መልኩ እንደምትወስዱት ድርሻችሁ”

ከአንተም ጋር ለዘርህ የጨው ቃል ኪዳን ለዘለላም ነው

ሁለቱ ሐረጎች የሚያመለክቱት ተመሳሳይ የሆነ ነገርን ነው፡፡“እነዚህ ሐረጎች በጋራ በመሆን አፅንዖት የሚሰጡት ኪዳኑ ለዘላለም የሚፀና መሆኑን ነው፡፡”“ዘላለማዊ የሆነ ሥምምነት”(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

የዘላለም ጨው ቃል ኪዳን

“በጨው የተደረገ ቃል ኪዳን”ጨው ዘለቂነትን የሚያመለክት ሲሆን በመሥዋዕትና በቃል ኪዳን ወቅት በሚደረጉ ምግቦች ላይ ጥቅም ላይ እንዲውል ይደረግ ነበር፡፡”ዘላቂነት ያለው ኪዳን”ወይም “ዘላለማዊ ኪዳን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በምድራቸው ርስት በመካከላቸውም ድርሻ አይሆንልህም

እግዚአብሔር ሌሎች ሰዎች የሚይዙትን ምድር እንደሚወርሱት ዓይነት አድርጎ ይናገራል፡፡“ከሕዝቡ ምድር አንዱንም አትወርሱም” ወይም “እሥራኤላውያን ከሚይዟቸው መሬቶች ውስጥ አንዱንም አትወስዱም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ድርሻህና ርስትህ ርስት እኔ ነኝ

እግዚአብሔር አሮንና ዘሩ እርሱን በክህነት በማገልገላቸው የሚጠብቃቸውን ታላቅ ክብር ሲገልፅላቸው ልክ እግዚአብሔር ራሱን እንደሚወርሱት አድርጎ ነው የሚናገረው፡፡“በዚያ ምትክ የምኖራችሁ እኔ ነኝ”ወይም“በዚያ ምትክ እንድታገለግሉኝ እፈቅድላችኋለሁ፤በአገልግሎታችሁም ወቅት የሚያስፈልጋችሁን ነገር ሁሉ አዘጋጅላችኋለሁ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:21

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ተመልከት ሰጥቼያለሁ

እዚህ ላይ“ተመልከት”የሚለው ቃል የሚቀጥለው ነገር ላይ የበለጠ አፅንኦት እንዲደረግ ያነሳሳል፡፡“በእርግጥ እኔ ሰጥቼያለሁ”

እንደ ርስታቸው

እግዚአብሔር አሮንና ዘሩ የሚቀበሉትን ነገር እንደሚወርሱት ዓይነት አድርጎ ነው የሚናገረው፡፡“ለእሥራኤል ሁሉ የምሰጠውን እንደ ድርሻቸው መጠን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:23

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለአሮን መናገሩን ይቀጥላል፡፡

በእሥራኤል ልጆች መካከል ርስት አይወርሱም

እግዚአብሔር ሌሎች የእስራኤል ሰዎች የሚይዙትን ምድር እንደሚወርሱት ዓይነት አድርጎ ይናገራል፡፡ሌዋውያን የትኛውንም ምድር አይቀበሉም”“ሌላው የእሥራኤል ሕዝብ የሚቀበለውን መሬት መቀበል አይኖርባቸውም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ ርስታቸው

እግዚአብሔር አሮንና ዘሩ የሚቀበሉትን ነገር እንደሚወርሱት ዓይነት አድርጎ ነው የሚናገረው፡፡“ለእሥራኤል ሁሉ የምሰጠውን እንደ ድርሻቸው መጠን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:25

ከእሥራኤል ልጆች ለእናንተ ርስት አድርጌ የሰጠኋችሁን አሥራት በተቀበላችሁ ጊዜ

የእሥራኤል ሕዝብ ከሰብሎቻቸውንና ከእንስሳቶቻቸው አንድ አሥረኛውን በሥጦታ መልክ ማቅረብ የሚጠበቅባቸው ሲሆን እግዚአብሔር ደግሞ ይሄንን ለሌዋውያን ይሰጣቸዋል፡፡

ለእናንተ ርስት ይሆን ዘንድ

የሚወርሱት ነገር ይመስል እግዚአብሔር አሮንና ትውልዱ ስለሚቀበለው ነገር እግዚአብሔር ይናገራል፡፡”ለእሥራኤል ሁሉ ከምሰጠው የእናንተ ድርሻ የሆነው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራታችሁን ማቅረብ ይኖርባችኋል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አሥራታችሁን ለመሥጠት ማሰብ ይገባችኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:28

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ሙሴ ለሌዋውያን መናገር የሚኖርበትን ነገር መናገሩን ይቀጥላል፡፡

የእርሱን የማንሣት ቁርባን ለካህኑ ለአሮን ትሰጣላችሁ

እዚህ ላይ“የእርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ነው፡፡በመሠረቱ የእግዚአብሔርን የማንሣት ቁርባንድርሻ መሥጠት የነበረባቸው ለእግዚአብሔር ነው፡፡“ለእግዚአብሔር መሥጠት የሚገባችሁን ቁርባንለአሮን መሥጠት ይኖርባችኋል”

ለአንተ የተሰጠህን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእሥራኤል ሕዝብ የሰጠህን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 18:30

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ከእርሱ የተመረጠውን

“ከእሥራኤል ሕዝብ ምርጥ የሆነውን ነገር የተቀበልከውን”

ሌሎች ሥጦታዎቻችሁ

“ሥጦታዎቹ”እሥራኤላውያን የሚያቀርቧቸው መሥዋዕቶች ሆነው ሌዋውያን የሚቀበሏቸው ነገሮች ናቸው፡፡

በመብላታችሁና በመጠጣታችሁ ምንም ዓይነት ኃጢአት አትሸከሙም

“እርሱን በምትበሉበትና በምትጠጡበት ወቅት በደለኞች አትሆኑም”


Chapter 19

1 ያህዌ ለሙሴና ለአሮን ተናገረ፤ እንዲህም አለ፣ 2 ”ይህ እናንተን የማዛችሁ ትዕዛዝ መታሰቢየ ነው፡፡ የእስራኤል ሰዎች ወደ አንተ ቀንበር ተጭኟት የማታውቅ፣ እንከን ወይም ነውር የሌለባት ቀይ ጊደር እንዲያመጡ ንገራቸው፡፡ 3 ጊደሯን ለካህኑ ለአልዓዛረ ስጠው፡፡ ከሰፈር ውጭ ያውጣት አንድ ሰው በፊቱ ይረዳት፡፡ 4 ካህኑ አልአዛር ከጊደሯ ደም በጣቱ ወስዶ በመገናኛው ድንኳን ፊት ባለው አቅጣጫ ሰባት ጊዜ ይርጨው፡፡ 5 ሌላ ካህን እርሱ እያየ ጊደሯን ያቃጥላት፡፡ ቆዳዋን፣ ስጋ እና ደሟን ከፈርሷ ጋር ያቃጥል፡፡ 6 ካህኑ የዝግባ እንጨት፣ ሂሶጵ፣ እና ደማቅ ሱፍ ይውሰድና ጊደሯ በምትቃጠልበት እሳት ውስጥ ይጨምር፡፡ 7 ከዚየ ልብሱን ይጠብ ሰውነቱንም በውሃ ይታጠብ፡፡ ከዚያ እስከ ምሽት እርኩስ ሆኖ ከቆየበት ወደ ሰፈር መመለስ ይችላል፡፡ 8 ጊደሯን ያቃጠለው ሰው ልብሱን በውሃ ይጠብ ገላውንም ይታጠብ፡፡ እስከ ምሽት እርኩስ ሆኖ ይቆያል፡፡ 9 ንጹህ የሆነ አንድ ሰው የጊደሯን አመድ አፍሶ ከሰፈር ውጭ ንጹህ በሆነ ስፍራ ይድፋው፡፡ ይህ አመድ ለእስራኤል ሰዎች ለማህበረሰቡ ይጠበቅ፡፡ አመዱ ከኃጢአት መስዋዕት የተገኘ እንደመሆኑ፣ ከኃጢአት ለመንጻት በውሃ ይበጠብጡታል፡፡ 10 የጊደሯን አመድ ያፈሰው ሰው ልብሱን ይጠብ፡፡ እስከ ምሽት እርኩስ ሆኖ ይቆያል፡፡ ይህ ለእስራኤላዊያንና ከእነርሱ ጋር ለሚኖሩ መጻተኞችም ቋሚ ህግ ይሆናል፡፡ 11 ማንም የሞተን ሰው አካል የነካ ሁሉ ለሰባት ቀናት እርኩስ ነው፡፡ 12 እንዲህ ያለው ሰው በሶስተኛውና በሰባተኛው ቀን ራሱን ያንጻ፡፡ ከዚያ ንጹህ ይናል፡፡ ነገር ግን በሶስተኛው ቀን ራሱን ካላነጻ፣ በሰባተኛው ቀን ንጹህ አይሆንም፡፡ 13 የሞተን ሰው የነካ ማንም ቢሆን፣ የሞተን ሰው የነካ ሁሉ፣ እናም ራሱን ያላነጻ ይህ ሰው የያህዌን ማደሪያ ያረክሳል፡፡ ያ ሰው ከእስራኤል ተለይቶ ይጥፋ፤ ምክንያቱም ከእርኩሰት የሚያነጻው ውሃ አልተረጨበትም፡፡ እርኩስ ሆኖ ይቆያል፣ ያለመንጻቱ በእርሱ ላይ ይቆያል፡፡ 14 አንድ ሰው በድንኳን ውስጥ በሚሞትበት ጊዜ ህጉ ይህ ነው፡፡ ወደ ድንኳኑ የገባ እያንዳንዱ ሰውና ቀድሞውኑም በድንኳኑ ውስጥ የነበረ ሰው ለሰባት ቀናት ንጹህ አይደለም፡፡ 15 ያልተከደነና ያልተሸፈነ ማናቸውም ዕቃ ይረክሳል፡፡ 16 በተመሳሳይ፣ በሰይፍ የተገደለንም ሰው ሆነ ማናቸውንም በሌላ ሁኔታ የሞተን ሰው፣ ወይም የሞተን ሰው አጽም፣ ወይም መቃብር የነካ ማናቸውም ከድንኳን ውጭ ያለ ሰው ለሰባት ቀናት ንጹህ አደለም፡፡ 17 ለረከሰ ሰው ይህን አድርግ፡ ከተቃጠለው የኃጢአት መስዋዕት ጥቂት አመድ ውሰድና በንጹህ ውሃ በዕቃ ውስጥ በጥብጠው፡፡ 18 ንጹህ የሆነ ሰው ሂሶጵ ይውሰድና ውሃው ውስጥ ይንከረው፤ ከዚያም በድንኳኑ ላይ፣ በድንኳኑ ውስጥ ባሉ ዕቃዎች ሁሉ ላይ፣ በዚያ በሚገኙ ሰዎች ላይ፣ እንዲሁም የሞተ ሰውን አጽም፣ የተገደለን ሰው፣ የሞተን ሰው ወይም መቃብር በነካ ሰው ላይ ይርጨው፡፡ 19 በሶስተኛው ቀንና በሰባተኛው ቀን፣ ንጹህ የሆነው ሰው ንጹህ ያልሆነውን ሰው ይርጨው፡፡ ያልነጻው ሰው በሰባተኛው ቀን ራሱን ያንጻ፡፡ ልብሱን ይጠብ ገላውንም በውሃ ይታጠብ፡፡ ምሽት ላይ ንጹህ ይሆናል፡፡ 20 ነገር ግን ሳይነጻ የሚቆይ ማናቸው ሰው፣ ራሱን ለማንጻት ያልፈቀደ ሰው ያ ሰው ከማህበረሰቡ ተለይቶ ይጥፋ፣ ምክንቱም የያህዌን መቅደስ አርክሷል፡፡ ከእርኩሰት የሚያነጻው ውሃ በእርሱ ላይ አልተረጨምና እርኩስ ሆኖ ይቆያል፡፡ 21 ለእነዚህ ሁኔታዎች ይህ ቀጣይ ህግ ይሆናል፡፡ ለመንጻት የሚሆንን ውሃ የሚረጨው ሰው ልብሶቹን ይጠብ፡፡ የሚያነጻውን ውሃ የሚነካ ሰው እስከ ምሽት ንጹህ አይደለም፡፡ 22 ማናቸውም ንጹህ ያልሆነ ሰው የነካው ነገር እርኩስ ይሆናል፡፡ ያንን የነካ ሰው እስከ ምሽት እርኩስ ይሆናል፡፡”



Numbers 19:1

ሥርዓት/ደንብ

በመሠረቱ እነዚህ ቃላት ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡“የሕግ ትዕዛዝ”ወይም “ሕጋዊነት ያለው ደንብ” (ሁለት ተመሳሳይ ገፅታ ያላቸው ነገሮች የሚለውን ይመልክቱ)

ለአንተ ያመጡልህ ዘንድ

እዚህ ላይ“ለአንተ”የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥር በመሆኑ የሚያመለክተው ሙሴን ነው፡፡

ቀንበር ያልተጫነች ወይም ነውርም የሌለባትን

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ቃላት ተመሣሣይ ዓይነት ትርጓሜ ያላቸው ሲሆኑ የሚያሳስበውም እንስሳው ምንም ዓይነት እንከን የማይገኝበት መሆን እንዳለበት አፅንኦት ለመሥጠት ነው፡፡(ሁለት ተመሳሳይ ገፅታ ያላቸው የሚለውን ይመልክቱ)

Numbers 19:3

በእርሱ ፊት

“በእርሱ እይታ ሥር”ወይም“ይመለከተው ዘንድ”

ካህኑ የዝግባ እንጨት መውሰድ ይኖርበታል

“ካህኑ የሚለው ቃል የሚያመለክተው አልዓዛርን ነው፡፡

ቀይ ግምጃ

“ደማቅ ቀይ ልብስ”

Numbers 19:7

ከዚያ በኋላ እርሱ ልብሱን ማጠብ ይኖርበታል

እዚህ ላይ“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አልዓዛርን ነው፡፡

ርኩስ ይሆናል

በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን አለማግኘት ወይም የተቀደሱ አገልግሎቶችን ለማከናወን ብቁ ያለመሆን ጉዳይ ሰውዬው ንፁሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ነው የሚነገረው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 19:9

ንፁሕ የሆነ ሰው

በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ማግኘትናወይም የተቀደሱ አገልግሎቶችን ለማከናወን ብቁ የመሆን ጉዳይ ሰውዬው ንፁሕ እንደሆነ ተደርጎ ነው የሚነገረው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አመዱ መከማቸት ይኖርበታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አመዶቹ መከማቸት ይኖርባቸዋል፡፡”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በንፁሕ ሥፍራ ላይ

በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ማግኘት ንፁሕ እንደመሆን ተደርጎ ነው የሚነገረው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ርኩስ ይሆናል

በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን አለማግኘት ወይም የተቀደሱ አገልግሎቶችን ለማከናወን ብቁ ያለመሆን ጉዳይ ሰውዬው ንፁሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ነው የሚነገረው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 19:11

አጠቃላይ መረጃ

“ንፁሕ መሆን”እና “መቀደስ” የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ማግኘትን ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አጠቃላይ መረጃ

“ንፁሕ ያልሆነ”“መርከስ”“ቅድሰና ማጣት” እና “በኃጢአት መበከል”የሚሉት ሃሣቦች የሚያመለክቱት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት አለማግኘትን ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የሞተውን ሰው በድን

“የማንኛውም ሰው ሬሣ”

ራሱን ያጠራል

ይሄ ሰው አንድ ንፁሕ የሆነ ሰው ይጠራና ከውኃ ጋር የተደባለቀ የጊደር አመድ በመርጨት እንዲያጠራው ይጋብዘዋል፡፡አንድን ሰው እንዲያጠራው በመጥራቱ ልክ ያ ሰው ራሱ እንደሚያጠራው ዓይነት ተደርጎ ነው የሚገለፀው፡፡“አንድን ሰው እንዲያጠራው መጋበዝ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በሶስተኛው ቀን ራሱን ካላጠራ በሰባተኛው ቀንም ንፁሕ አይሆንም

ይሄ በአዎንታዊ መልኩ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በሰባተኛው ቀን ንፁሕ የሚሆነው በሶስተኛው ቀን ራሱን ያጠራ እንደሆነ ብቻ ነው”(ድርብ አሉታዎች)

ያ ሰው ተለይቶ መጥፋት አለበት

“መጥፋት”የሚል ቃል የሚያመለክተው ከማህበረሰቡ ጋር ያለው ማንኛውም ግንኙነት ተቋርጦ መባረሩን ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 9፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ያ ሰው መባረር አለበት”ወይም “ያንን ሰው ማባረር አለባችሁ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በእርሱ ላይ ባለው ርኩሰት ላይ ውኃ አልተረጨምና

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ማንም ሰው በርኩሰቱ ላይ ውኃን አልረጨም”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በርኩሰት ላይ የሚረጭ ውኃ

“የረከሱ ነገሮች እንዲነፁ ለማድረግ የሚረጭ ውኃ”ወይም“ነገሮችን ለማንፃት የሚረጭ ውኃ”

ርኩስ ይሆናል፤ርኩሰቱ ከእርሱ ጋር ይቆያል

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን በአንድ ላይ እንዲነገሩ የተደረገው ለጉዳዩ አፅንኦት ለመስጠት ሲባል ነው፡፡ (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 19:14

አጠቃላይ መረጃ

“ንፁሕ ያልሆነ”የሚለው ሃሣብ የሚያመለክተው በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት አለማግኘትን ወይም ለአገልግሎት ብቁ አለመሆንን ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

መክደኛው ያልታሰረ የተከፈተ ዕቃ ሁሉ ርኩስ ይሆናል

ይሄ በአዎንታዊ መልኩ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የተከፈቱ ዕቃዎች ንፁሕ የሚሆኑት መሸፈኛ የሚደረግላቸው ከሆነ ብቻ ነው፡፡“ድርብ አሉታዊነት”

በሠይፍ የተገደለ ሰው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሌላ ሰው በሠይፍ የገደለው ሰው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 19:17

አጠቃላይ መረጃ

“ንፁሕ ያልሆነ”የሚለው ሃሣብ የሚያመለክተው በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት አለማግኘትን ወይም ለአገልግሎት ብቁ አለመሆንን ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አጠቃላይ መረጃ

“ንፁሕ መሆን”እና “መቀደስ” የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ማግኘትን ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 19:20

አጠቃላይ መረጃ

“ንፁሕ መሆን”እና “መቀደስ” የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት መኖሩን ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አጠቃላይ መረጃ

“ንፁሕ ያልሆነ”የሚለው ሃሣብ የሚያመለክተው በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት አለማግኘትን ወይም ለአገልግሎት ብቁ አለመሆንን ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 20

1 የእስራኤል ሰዎች፣ መላው ማህበረሰብ በመጀመሪያው ወር ወደ ሲና ምድረ በዳ ሄደው በቃዴስ ሰፈሩ፡፡ማርያም በዚያ ሞታ ተቀበረች፡፡ 2 ማህበረሰቡ ውሃ ተጠማ፣ ስለዚህ በሙሴና በአሮን ላይ አምጸው ተሰበሰቡ፡፡ 3 ህዝቡ በሙሴ ላይ አጉረመረሙ፡፡ እንዲህም አሉ፣ “ወገኖቻችን እስራኤላውያን በያህዌ ፊት በሞቱበት ጊዜ እኛም ብንሞት ኖሮ ይሻል ነበር! 4 እዚህ እንሞት ዘንድ የያህዌን ማህበረሰብ፣ እኛንና ከብቶቻችንን ለምን ወደዚህ ምድረበዳ አመጣችሁን? 5 ወደዚህ አስፈሪ ስፍራ ልታመጡን ለምን ከግብጽ እንድንወጣ አደረጋችሁን? እዚህ፤ እህል፣ በለስ፣ ወይም ወይም ሮማን የለም፡፡ የሚጠጣም ውሃ የለም፡፡” 6 ስለዚህ ሙሴና አሮን ከጉባኤው ፊት ወጥተው ሄዱ፡፡ ወደ መገናኛው ድንኳን መግቢያ ሄደው በግምባራቸው ተደፉ፡፡ ከዚያ የያህዌ አንጸባራቂ ክብር ታያቸው፡፡ 7 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 8 “በትርህን ውሰድና አንተና ወንድምህ አሮን ማህበረሰቡን ሰብስቡ፡፡ በፊታቸው ለዓለቱ ተናገር፣ ውሃ እንዲያፈስም አለቱን እዘዘው፡፡ ከዚያ ዓለት ውሃ አውጥተህ ትሰጣቸዋለህ፣ ማህበረሰቡና ከብቶቻቸው ይጠጡ ዘንድ ውሃ ስጣቸው፡፡” 9 ሙሴ ያህዌ እንዳዘዘው ከያህዌ ፊት በትሩን ወሰደ፡፡ 10 ከዚያ ሙሴና አሮን ጉባኤውን በአለቱ ፊት ሰበሰቡ፡፡ ሙሴ ጉባኤውን እንዲህ አለ፣ “እናንተ አመጸኞች፣ አሁን ስሙ፡፡ ከዚህ ዓለት ለእናንተ ውሃ ማውጣት አለብን?” 11 ከዚያ ሙሴ እጁን አንስቶ በበትሩ አለቱን ሁለት ጊዜ መታው፣ እናም ብዙ ውሃ ወጣ፡፡ ማህበረሰቡ ጠጣ፣ እንዲሁም ከብቶቻቸው ጠጡ፡፡ 12 ከዚያ ያህዌ ሙሴንና አሮንን እንዲህ አላቸው፣ “እኔን ስላላመናችሁ ወይም በእስራኤል ሰዎች ዐይኖች ፊት ቅዱስ አድርጋች ስላለያችሁኝ፣ ይህን ጉባኤ ወደ ሰጠኋችሁ ምድር አታስገቧቸውም፡፡” 13 ይህ ቦታ የመሪባ ውሃ ተብሎ ተጠራ፣ ምክንያቱም በዚያ የእስራኤል ሰዎች ከያህዌ ጋር ተጣልተው ነበር፣ እርሱም ራሱን በቅድስናው ገለፀላቸው፡፡ 14 ሙሴ ከቃዴስ መልዕክተኞችን ወደ ኤዶም ንጉስ ላከ፡ ወንድምህ እስራኤል ይህን ይላል፡ “በእኛ ላይ የደረሱትን አስቸጋሪ ነገሮች ታውቃለህ፡፡ 15 አባቶቻችን ወደ ግብፅ ወርደው ለዘመናት በግብጽ መኖራቸውን ታውቃለህ፡፡ ግብጻውያን በእኛና በአባቶቻችን ላይ እጅግ ከፉብን፡፡ 16 እኛ ወደ ያህዌ ስንጮህ፣ እርሱ ድምጻችንን ሰምቶ መልዓክ ልኮ ከግብጽ አወጣን፡፡ እነሆ፣ በምድርህ ዳርቻ በምትገኘው በቃዴስ እንገኛለን፡፡ 17 በምድርህ እንድናልፍ እንድትፈቅድልን እጠይቅሃለሁ፡፡ በእርሻዎች ወይም በወይን ሥፍራዎች ውስጥ አናልፍም፣ አሊያም ከጉድጓዶቻችሁ ውሃ አንጠጣም፡፡ የንዱን አውራ ጎዳና ይዘን እንሄዳለን፡፡ ድንበርህን እስክናልፍ ድረስ ወደ ግራም ወደ ቀኝም አንልም፡፡” 18 የኤዶም ንጉስ ግን እንዲህ ሲል መለሰለት፣ “በዚህ በኩል ማለፍ አትችሉም፡፡ ይህን ብታደርጉ፣ ሰይፍ ይዤ እወጣባችኋለሁ፡፡” 19 ከዚያ የእስራኤል ሰዎች እንዲህ አሉት፣ “እኛ በአውራ ጎዳናው እንሄዳለን፡፡ እኛም ሆን ከብቶቻችን ውሃህን ብንጠጣ፣ ለዚያም እንከፍላለን፡፡ ሌላ ምንም ነገር ሳናደርግ በእግራችን እንለፍ፡፡” 20 የኤዶም ንጉስ ግን እንዲህ ሲል መለሰ፣ “በዚህ በኩል አታልፉም፡፡” ስለዚህም የኤዶም ንጉስ በብርቱ ክንድ አያሌ ወታደሮች ይዞ በእስራኤላዊያን ላይ መጣባቸው፡፡ 21 የኤዶም ንጉስ እስራኤላውያን በድንበሩ አቋርጠው እንዳያልፉ ተቃወመ፡፡ በዚህ ምክንያትና እስራኤል ከኤዶም ምድር ተመለሱ፡፡ 22 ስለዚህ ህዝቡ ከቃዴስ ተነስቶ ተጓዘ፡፡ የእስራኤል ህዝብ፣ መላው ማህበረሰብ ወደ ሖር ተራራ መጣ፡፡ 23 ያህዌ በሖር ተራራ ለሙሴና አሮን ተናገራቸው፡፡ እንዲህም አለ፣ 24 ”አሮን ለእስራኤል ህዝብ ወደ ሰጠኋት ምድር አይገባምና ወደ አባቶቹ ይሰበሰባል፡፡ ይህም የሚሆነው እናንተ ሁለታችሁም በመሪባ ውሃ በእኔ ቃሎች ላይ ስላመፃችሁ ነው፡፡ 25 አሮንንና ልጁን አልዓዛርን ይዘህ ወደ ሖር ተራራ አምጣቸው፡፡ 26 የአሮንን የክህነት ልብስ ከእርሱ ላይ አውልቀህ ልጁን አልዓዛርን አልብሰው፡፡ አሮን በዚያ ይሞትና ወደ ወገኖቹ ይሰበሰባል፡፡” 27 ሙሴ ያህዌ እንዳዘዘው አደረገ፡፡ መላው ማህበረሰብ እያየ ወደ ሖር ተራራ ወጡ፡፡ 28 ሙሴ የአሮንን የክህነት ልብሶች ከእርሱ አውልቆ ልጁን አልዓዛርን አለበሰው፡፡ አልዓዛር በተራራው አናት ላይ በዚያ ሞተ፡፡ ከዚያ ሙሴና አልዓዛር ከተራራው ወደ ታች ወረዱ፡፡ 29 መላው ማህበረሰብ አሮን እንደ ሞተ ባየ ጊዜ፣ ጠቅላላው አገሩ ለሰላሳ ቀናት ለአሮን አለቀሰ፡፡



Numbers 20:1

የፂን ምደረ በዳ

እዚህ ላይ “ፂን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በዕብራይስጥምድረ በዳ የሚለውን ሥያሜ ነው፡፡(ቃላትን መቅዳት ወይም መዋስ የሚለውን ይመልከቱ)

የመጀመሪያው ወር

በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት ይሄየመጀመሪያ ወራቸው ነው፡፡እግዚአብሔር ከግብፃውያን ነፃ ያወጣቸውን ጊዜ የሚያመለክት ነው፡፡በምዕራባውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት የመጀመሪያ ወር የሚሆነው በመጋቢት የመጀመሪያዎቹ ቀናትና በየካቲት የመጀመሪያዎቹ ቀናት ወቅት ነው፡፡(የዕብራውያን ወራት የሚለውን ይመልከቱ)

ተቀበረች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ቀበሯት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:2

እነርሱ ተሰበሰቡ

እዚህ ላይ “እነርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ማህበረሰቡን ነው፡፡

በአንድነት ተሰበሰቡ

“ለአመፅ ተሰባሰቡ”

በእግዚአብሔር ፊት

ይሄ የሚያመለክተው በእግዚአብሔር ድንኳን ፊት መሆናቸውን ነው፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:4

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

የእሥራኤል ሕዝብ በሙሴና በአሮን ላይ ማጉረምረማቸውን ይቀጥላሉ፡፡

የእግዚአብሔርን ሕዝብ ወደ ምድረ በዳ ለምን አመጣህ? እኛና ከብቶቻችን እንድንሞት ነውን?

ሕዝቡ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው በሙሴና በአሮን ላይ ለማጉረምርም ነው፡፡እንደ መግለጫ ሊታይ ይችላል፡፡“የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከከብቶቹ ጋር እንዲሞት ለማድረግ እዚህ በረሃ ውስጥ ማምጣት አልነበረብህም” (ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ወደዚህ አስከፊ ሥፍራ እንመጣ ዘንድ ከግብፅ ምድር ለምን አወጣኸን?

ሕዝቡ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው በሙሴና በአሮን ላይ ለማጉረምርም ነው::እንደ መግለጫ ሊታይ ይችላል፡፡“እኛን ወደዚህ አስከፊ ሥፍራ ለማምጣት ከግብፅ ምድር ልታወጣን አይገባህም ነበር”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:6

በግምባራቸው ተደፉ

ይሄ የሚያመለክተው ሙሴና አሮን በእግዚአብሔር ፊት ራሣቸውን ማዋረዳቸውን ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:7

በዓይናቸው ፊት

እዚህ ላይ ሰዎቹ የሚያዩትን ነገር በሚመለከት“ዓይናቸው”እንደ ወኪል ሆኖ ቀርቧል፡፡“አንተን በሚመለከቱበት ወቅት”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ፊት

ይሄ የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ድንኳን ነው፡፡“ከእግዚአብሔር ድንኳን”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:10

ከዚህ ድንጋይ ውኃ እናውጣላችሁን?

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው ከብስጭት የተነሣ ሲሆን ሕዝቡ በማጉረምረማቸው ሊገስፃቸው ነበር፡፡ይሄ እንደ መግለጫ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ውኃ የለም ብላችሁ አጉረምርማችኋል፡፡እንደዚህ ከሆነ ከዚህ ዓለት ውኃ እናወጣላችኋለን”ወይም“ከዚህ ዓለት ውኃ ብናወጣላችሁ እንኳን ደስተኞች አትሆኑም፡፡ቢሆንም ግን አደርገዋለሁ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

እኛ ማውጣት አለብን?

እዚህ ላይ“እኛ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴንና አሮንን ሲሆን እግዚአብሔርንም የሚያካትት ሊሆን ይችላል፡፡ሆኖም ግን ሕዝቡን አያካትትም፡፡(“እኛ”የሚለውንና አካታችና አካታች ያልሆነውን የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:12

በእሥራኤል ልጆች ዓይኖች ፊት ትቀድሱኝ ዘንድ በእኔ አላመናችሁም

እዚህ ላይ ሙሴ በእግዚአብሔር ላይ አለመታመኑና እግዚአብሔርን ያለማክበሩ ነገር በእርሱ ላይ መታየቱ በግልፅ ሊብራራ ይችላል፡፡“በእሥራኤል ልጆች ዓይኖች ፊት ትቀድሱኝ ዘንድ በእኔ ባለማመናችሁምክንያት እኔ በተናገርኩት መንገድ ልታደርግ ሲገባህ በራስህ ሃሣብ ተመስርተህ ዓለቱን መታህ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሥራኤል ዓይኖች ፊት

እዚህ ላይ ሰዎቹ የሚያዩትን ነገር በሚመለከት “ዓይናቸው”እንደ ወኪል ሆኖ ቀርቧል፡፡“አንተን በሚመለከቱበት ወቅት”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

የዚህ ሥፍራ ሥም

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰዎች ይሄንን ሥፍራ የሚጠሩት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:14

ወንድምህ እሥራኤል

ሙሴ ይሄንን ሐረግ የተጠቀመበት ምክኒያት ዘሮቻቸው የሆኑት ያዕቆበና ኤሳው ወንድማማቾች ስለሆኑ እሥራኤላውንና ኤዶማውያን ዘመዳሞች እንደሆኑ አፅንዖት ለመስጠት ፈልጎ ነው፡፡

ወደ እግዚአብሔርም በጮሀን ጊዜ

“ዕርዳታ ያደርግልን ዘንድ ወደ እግዚአብሔር በፀለይን ጊዜ”

ድምፃችንን ሰማ

እዚህ ላይ“ድምፅ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው መጮሃቸውንና ለእርሱ የተናገሩትን ነገር ነው፡፡“ጩኸታችንን አዳመጠ”ወይም “የጠየቅነውን ነገር ሰማን”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

እነሆ

“እነሆ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ስላለፈው ነገር ማውራት ማቆማቸውንና አሁን ስላሉበት ሁኔታ እየተናገሩ መሆኑን ይገልፃል፡፡

Numbers 20:17

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

መልዕክተኞቹ ስለ ኤዶም ንጉሥ መናገራቸውን ይቀጥላሉ፡፡

ወደ ቀኝም ወደ ግራም አንልም

“አንልም”የሚለው ቃል የሚያመለክተው መንገድ መልቀቅን ነው፡፡“በየትኛውም አቅጣጫ ቢሆን መንገዱን አንለቅም”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በንጉሡ ጎዳና

ይሄ ሰሜናዊውን የደማስቆ የሰሜኑን ክፍል ክፍል በደቡብ ከሚገኘው የአካባ ባህረ ሰላጤ ጋርየሚያገናኝ ዋና መንገድ ነው፡፡

Numbers 20:18

በሠይፍ እንዳልገጥምህ አንተ በምድሬ ላይ አታልፍም

“አንተ”የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥር በመሆኑ የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ የሚወክለውን ሙሴን ነው፡፡“ሕዝብህን በሠይፍ እንዳልገጥም አንተ በምድሬ ላይ አታልፍም”(አንተ/እናንተ የሚለው ቃል በተለያየ መንገድ የሚገለፅበት የሚለውንና ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

በሠይፍ እንዳልገጥም

እዚህ ላይ “ሠይፍ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የንጉሡን ሠራዊት ነው፡፡“ሠራዊቴን እልካለሁ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል ሕዝብ

ይሄ ሐረግ የሚያመለክተው የእሥራኤልን መልዕክተኞች ነው፡፡

በእግራችን እንለፍ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው በዚያ በኩል በእግራቸው ለማለፍ እንደፈለጉ ብቻ ነው፡፡የኤዶምን ህዝብ ለማጥቃት በሠረገሎች አይመጡም ማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:20

ኤዶምያስም በብዙ ሕዝብና በፅኑ እጀ ሊገጥመው ወጣ

እዚህ ላይ እጅ የሚለው ቃል የሚያመለከተው የንጉሡን ጠንካራ ሠራዊት ነው፡፡“የኤዶም ንጉሥ እሥራኤልን ይዋጉ ዘንድ ብዙ ተዋጊዎች ያሉበትን ጠንካራ ሠራዊት ላከ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በእነርሱ ድንበር ላይ ማለፍ

እዚህ ላይ “እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አዶማውያንን ነው፡፡

Numbers 20:22

የእሥራኤል ልጆች ማህበር ሁሉ

“ማህበር ሁሉ”የሚለው ቃል የሚሰጠው ያለምንም ልዩነት እዚያ የተገኘና “የእሥራኤል ሕዝብ”አካል የሆነ እያንዳንዱ ግለሰብ እዚያ ስለመገኘቱ አፅንኦት ይሰጣል፡፡ (ሁለት ተመሳሳይ ገፅታ ያላቸው የሚለውን ይመልክቱ)

አሮን ወደ ወገኑ ይከማች

ይሄ ጨዋ በሆነ አነጋገር አሮን መሞት አለበት ማለት ነው፡፡ይሄ የሚያመለክተው አሮን መሞት ያለበት መሆኑንና መንፈሱም አባቶቹ ወዳሉበት ሥፍራ መሄድ ያለበት መሆኑን ነው ፡፡“አሮን መሞተ አለበት”(ሥርዓት የሌለውን ነገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

በቃሌ ስላመፃችሁ

“እኔ የተናገርኩትን ተግባራዊለማድረግ እምቢ አላችሁ”

Numbers 20:25

ማያያዣ ዓረፍተ ነገር

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ወደ ወገኑ ይከማች፤በዚያም ይሙት

በመሠረቱ እነዚሀ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡ይሄ የሚያመለክተው አሮን መሞት ያለበት መሆኑንና መንፈሱም አባቶቹ ወዳሉበት ሥፍራ መሄድ ያለበት መሆኑን ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውንና ሥርዓት የሌለውን ነገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 20:27

ሠላሣ ቀናት

“30 ቀናት”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 21

1 በኔጌብ የሚኖረው ከነዓናዊው የዓረድ ንጉስ እስራኤል ወደ አታሪም እየመጣ በመንገድ ላይ መሆኑን ሲሰማ፣ ከእስራኤል ጋር ተዋግቶ አንዳንዶቹን በምርኮ ወሰደ፡፡ 2 እስራኤል ለያህዌ እንዲህ ብሎ ማለ፣ “በእነዚህ ህዝቦች ላይ ድል ብትሰጠን፣ ከዚያም ከተማቸውን ሙሉ ለሙሉ እናጠፋለን፡፡” 3 ያህዌ የእስራኤልን ድምጽ ሰምቶ በከነዓናዊያን ላይ ድልን ሰጣቸው፡፡ ሙሉ ለሙሉ እነርሱንና ከተማቸውን አጠፉ፡፡ ያ ስፍራ ሖርማ ተብሎ ተጠራ፡፡ 4 ከሖር ተራራ ተነስተው ኤዶም ምድር ዙሪያ ለመድረስ በቀይ ባህር መንገድ ተጓዙ፤ ህዝቡ በመንገድ ሳለ እጅግ ተስፋ ቆረጡ፡፡ 5 በእግዚአብሔርና በሙሴ ላይ እንዲህ ሲሉ አጉረመረሙ፡፡ “በበረሃ እንሞት ዘንድ ለምን ከግብጽ አወጣችሁን በዚህ ዳቦ የለም፣ አንዳች ውሃ የለም፣ ደግሞም ይህን የማይረባ ምግብ ጠልተነዋል፡፡” 6 ከዚያ ያህዌ በሰዎቹ መካከል መርዛም እባቦችን ሰደደ፡፡ እባቦቹ ሰዎችን ነደፉ፤ ብዙ ሰዎችም ሞቱ፡፡ 7 ሰዎች ወደ ሙሴ መጥተው እንዲህ አሉ፣ “እኛ በድለናል ምክንያቱም በያህዌና በአንተ ላይ በተቃውሞ ተናግረናል፡፡ እባቦቹን ከእኛ እንዲያርቅ ወደ ያህዌ ጸልይልን፡፡” ስለዚህም ሙሴ ለህዝቡ ጸለየ፡፡ 8 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “እባብ አብጅና በምሰሶ ላይ አንጠለጠለው፡፡ እንዲህ ይሆናል፣ የተነደፈ ሁሉ ያንን ከተመለከተ ይድናል፡፡” 9 ስለዚህም ሙሴ የናስ እባብ አበጅቶ በምሰሶ ላይ አንጠለጠለው፡፡ እባብ ማናቸውንም ሰው በነከሰ ጊዜ፣ ሰውየው ወደ ናሱ እባብ ከተመለከተ ይድናል፡፡ 10 ከዚያ የእስራኤል ሰዎች ተጉዘው በአቦት ሰፈሩ፡፡ 11 ከአቦት ተጉዘው በስተምስራቅ በሞአብ አንጻር በዒዮዓባሪም በምድረ በዳ ሰፈሩ፡፡ 12 ከዚያ ተጉዘው በዘሬድ ሸለቆ ሰፈሩ፡፡ 13 ከዚያ ተጉዘው እስከ አሞራዊያን ድንበር በሚዘልቀው በምድረበዳ ባለው በአሮን ወንዝ ሌላኛው ዳርቻ ሰፈሩ፡፡ የአርኖን ወንዝ በሞዐብና አሞራዊያን መሀል የሞአብን ወሰን ያበጃል፡፡ 14 በያህዌ የጦርነት መጽሐፍ ጥቅልል፣ በሱፋ ውስጥ የሚገኘው ዋሄብ እና የአርኖን ሸለቆዎች፣ 15 ወደ ዔር ከተማና ወደ ሞአብ ዳርቻ የሚወስዱ የሸለቆዎች ቁልቁለት” ተብሎ የተፃፈው ስለዚህ ነው፡፡ 16 ከዚያ ተነስተው ወደ ብኤር ተጓዙ፣ ይህም ስፍራ የውሃ ጉድጓድ የሚገኝበትና ያህዌ ሙሴን፡ - “ውሃ እሰጣቸው ዘንድ ሰዎቹን በአንድነት ሰብስባቸው” ብሎ የተናገረበት ነው፡፡ 17 ከዚያ እስራኤል ይህን መዝሙር ዘመረ፡፡ “አንተ ምንጭ ሆይ ፍለቅ፡፡ ስለዚህ እናንተም ዘምሩ፡፡ 18 መሪዎቻችን የቆፈሩት ጉድጓድ፣ የተከበሩ የህዝብ አለቆች በበትረ መንግስታቸውና በበትሮቻቸው የማሱት ጉድጓድ፡፡” ከዚያ ከምድረበዳው ተነስተው ወደ መቴና ተጓዙ፡፡ 19 ከመቴና ተነስተው ወደ ነሃሊኤል፣ ከነሃሊኤል ወደ ባሞት እና ከባሞት በሞአብ ምድር ወደሚገኘው ሸለቆ ተጓዙ፡፡ 20 በፈስጋ ተራራ ጫፍ ሆኖ ምድረበዳው ቁልቁል የሚታይበት ይህ ስፍራ ነው፡፡ 21 ከዚያ እስራኤል ወደ አሞራዊያን ንጉስ ወደ ሴዎን እንዲህ ብለው መልእክተኞችን ላኩ፣ 22 ”በምድርህ እንለፍ፡፡ ወደ እርሻዎች ወይም ወደ ወይን አትክልቶች አንገባም፡፡ ከጉድጓዶችህ ውሃ አንጠጣም፡፡ ድንበርህን እስክናልፍ ድረስ በንጉሱ አውራ መንገድ እንጓዛለን፡፡” 23 ንጉስ ሴዎን ግን እስራኤልን በድንበሩ እንዲያልፉ አልፈቀደም፡፡ ይልቁንም፣ ሴዎን ወታደሮቹን አሰባስቦ በምድረ በዳ እስራኤልን ለመውጋት ወጣ፡፡ 24 እስራኤል የሴዎንን ጦር በሰይፍ ወግቶ ከአርኖን እስከ ያቦቅ ወንዝና እስከ አሞን ሰዎች ወሰን ድረስ ምድሩን ወሰደ፡፡ የአሞን ሰዎች ድንበር ግን የተመሸገ ነበር፡፡ 25 እስራኤል የአሞራዊያንን ከተሞች ሁሉ፣ ሐስቦንንና መንደሮቹን ጭምር ይዞ በእነዚያ ውስጥ ተቀመጠ፡፡ 26 ሐስቦን ከሞአብ የቀድሞ ንጉስ ጋር የተዋጋው የአሞራዊያን ንጉስ የሴዎን ከተማ ነበረች፡፡ ሴዎን እስከ አርኖን ወንዝ ድረስ ያለውን ምድሩን ሁሉ ወሰደበት፡ 27 በምሳሌያዊ ንግግር የተናገሩ፣ “ወደ ሐሴቦን ኑ፡፡ የሴዎን ከተማ እንደ ገና ትገንባና ዳግም ትታነጽ፡፡ 28 እሳት ከሐሴቦን ተንቦገቦገ፣ ነበልባል ከሴዎን ከተማ የሞአብን ዔር አጠፉ፣ ደግሞም የአርን ተራሮች ባለቤቶችን በላ፡፡ 29 ሞአብ ዋይታ ሆነብህ! የከሞስ ህዝብ እናንተ ጠፋችሁ፡፡ ለአሞራውያን ንጉስ ለሴዎን ወንዶች ልጆቹን ለሽሽት ሴቶች ልጆቹን ለምርኮ አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ 30 እኛ ግን ሴዎንን አሸንፈናል፡፡ ሐስቦን እስከ ዴናን ድረስ ወድማለች፡፡ ወደ ሜድባ እስከምታደርሰው ኖፋ ድረስ ሁሉንም አሸንፈናቸዋል፡፡” 31 ስለዚህ እስራኤል በአሞራዊያን ምድር መኖር ጀመረ፡፡ 32 ከዚያ ሙሴ ሰዎችን ምድሪቱን እንደያዙ ወደ ኢያዜር ላከ፡፡ እነርሱ መንደሮቿን ማረኩ በዚያ የነበሩትንም አሞራዊያን አባረሩ፡፡ 33 ከዚያ ወደ ባሳን በሚስደው መንገድ ዞረው ሄዱ፡፡ የባሳን ንጉስ ዐግ በእነርሱ ላይ ዘመተ፣ እርሱና ሰራዊቱ ሁሉ በኤድራይ ሊዋጓቸው ወጡ፡፡ 34 በዚያን ጊዜ ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “እርሱን አትፈራው፣ ምክንያቱም እኔ በእርሱ፣ በሰራዊቱና በምድሩ ላይ ሁሉ ላይ ድል ሰጥቼሃለሁ፡፡ በሔስቦን እንደነበረው በአሞራዊያን ንጉስ በሴዎን ላይ እንዳደረከው በእርሱ ላይ አድርግበት፡፡” 35 ስለዚህም እርሱን፣ ወንዶች ልጆቹን እና መላውን ሰራዊቱን አንድም ሰው በህይወት እስከ ማይተርፍለት ድረስ ፈጇቸው፡፡ ከዚያም ምድሩን ወረሱ፡፡



Numbers 21:1

ከእሥራኤልም ጋር ሠልፍ አደረገ

“ሠልፍ አደረገ”ማለት ሠራዊቱ ተዋጋ ማለት ነው፡፡“የእርሱ ሠራዊት ከእሥራኤል ሕዝብ ጋር ተዋጋ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ስእለት ተሳለ

ይሄ የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡“የእሥራኤል ሕዝብ ስእለትን ተሳለ”ወይም “እሥራኤላውያን ስእለትን ተሳሉ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤልን ድምፅ ሰማ

“ሰማ”ማለት የጠየቁትን ነገር አደረገላቸው ማለት ነው፡፡“እሥራኤል ጥያቄ ባቀረበለት መሠረት ተግባራዊ አደረገው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል ድምፅ

እዚህ ላይ “ድምፅ”የሚለው ቃልከጥያቄያቸው ጋር የተያያዘ አባባል ነው፡፡“እሥራኤል የጠየቀውን”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ከተሞቻቸውንም እርም ብለው አጠፉ

“የእሥራኤል ሕዝብ የከነዓናውያንን ሠራዊትና ከተሞቻቸውን ፈፅሞ አጠፉ”

የዚያን ሥፍራ ሥም ሔርማ ብለው ጠሩት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ያንን ሥፍራ ሔርማ ብለው ጠሩት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:4

በምድረ በዳ እንሞት ዘንድ ከግብፅ ለምን አወጣችሁን?

ሕዝቡ ይሄንን ጥያቄ የጠየቀው ሙሴን ለመገሰፅ ነበር፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እኛን በምድረ በዳ ለመግደል ከግብፅ ልታወጣን አይገባህም ነበር”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:6

በእግዚአብሔርና በአንተ ላይ ተናግረናል፡፡

“በእግዚአብሔርና በአንተ ላይ ክፉ ነገርን ተናግረናል”

እኛ ተናግረናል…ከእኛ

“እኛ”እና “ከእኛ”የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት ሙሴን ሣይሆን ሕዝቡን ነው፡፡(“እኛ”የሚለውንና አካታች ሆነውንና ያልሆነውን የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:8

እባብን ሥራ

ሙሴ እውነተኛ የሆነ እባብን መሥራት የማይችል በመሆኑ የእባብ ናሙና እንዲሰራ ነበር የተፈለገው፡፡ይሄ ተግባራዊ መሆን ያለበት መረጃ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“የእባብ ምሳሌን ሥራ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የተነደፈውም ሁሉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እባብ የሚነድፈው ሰው በሙሉ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የናስ እባብ

“ከነሐስ የሰራ እባብ”

እባብም የነደፈችው ሁሉ የናሱን እባብ ባየ ጊዜ እርሱ ዳነ

እዚህ ላይ “እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በእባብ የተነደፈውን “ማንኛውንም ሰው”ነው፡፡

Numbers 21:10

በሞአብ ፊት ለፊት

እዚህ ላይ “ፊት ለፊት”የሚለው ቃል ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን “ከእነርሱ ማዶ”ወይም “ከእነርሱ አጠገብ”ማለት ነው፡፡“ከሞአብ በመቀጠል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:12

በሞአብና በአሞራውያን መካከል ያለ የሞአብ ዳርቻ ነው

ይሄ ማለት እነዚህ ሁለት ሕዝቦች እንደ ድንበር በሚያገለግላቸው በወንዙ አጠገብ ባሉ ክፍሎች ላይ ይኖሩ ነበር ማለት ነው፡፡አሞራውን በወንዙ ደቡብ ክፍል ሲኖሩ አሞራውያን ደግሞ በወንዙ የሰሜኑ ክፍል ነበር የሚኖሩት፡፡

Numbers 21:14

ዋሄብ በሱፋ

እነዚህ ሁለቱም የቦታ ሥሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የአርኖንም ሸለቆዎች ወደ ኤር ማደሪያ የሚወርድ በሞአብም ዳርቻ የሚጠጋ

“ወደ አርኖን ከተማ የሚያመራውና በሞአብ ድንበር ላይ ተንጣሎ የሚገኘው ሸለቆ“

Numbers 21:16

ብኤር፤ጉድጓዱ

እነዚህ እንደ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ሊገለፁ ይችላሉ፡፡“ወደ ብኤር፤በዚያ ጉድጓድ ነበረ”

ይኸውም እግዚአብሔር ሙሴን “ሕዝቡን ሰብስብ ውኃንም እሰጣቸዋለሁ ብሎ የተናገረበት ነው”

ይሄ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ጥቅስ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ይኸውም እግዚአብሔር ሙሴን “ሕዝቡን ወደ እርሱ እንዲሰበስብ አድርጎ ውኃን ለመሥጠት የተናገረበት ነው”(ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆኑ አባባሎች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:17

አንተ ምንጭ ሆይ ፍለቅ

“ምንጭ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በጉድጓድ ውስጥ ያለውን ውኃ ነው፡፡እሥራኤላውያን የሚያዳምጣቸው ሰው ይመስል ለውኃው የሚናገሩ ሲሆን ጉድጓዱን እንዲሞላላቸው ይጠይቁታል፡፡“አንተ ውኃ ጉድጓዱን ሙላ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውንና ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

የሕዝብ አዛውንቶች ያጎደጎዱት፤አለቆችም የቆፈሩት

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ውኃውን በመቆፈር ረገድ መሪዎች ያላቸውን ሚና አፅንኦት በመሥጠት ይናገራል፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

በበትረ መንግሥት፤በበትራቸውም

በትረመንግሥትየያዝየነበረውሥልጣንበነበራቸውሰዎችሲሆንበትርደግሞይያዝየነበረውበሁሉምሰውነበር፡፡እነዚህሁለቱለቁፋሮአገልግሎትየሚውሉመሣሪያዎችአይደሉም፡፡እነዚህሁለትቁሣቁሶች የሚያሣዩት በአካባቢያቸውየሚገኙትን ነገሮች ለመጠቀም ኩራት የሚባል ነገር የሌለባቸው ስለመሆኑ አፅንኦት ለመስጠት ነው፡፡“በትረ መንግሥታቸውንና በትራቸውን እንኳን ሳይቀር ይጠቀማሉ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:19

ነሃልኤል…ባሞት

እነዚህ የቦታ ሥሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ፈስጋ ተራራ

ይሄ የተራራ ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ምድረ በዳውን ከላይ ወደሚመለከተው

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡ይሄ አነጋገር ተራራው ከፍ ያለ እንደሆነ ለመግለፅ ሲሆን ተራራው ከሥሩ የሚገኘውን ምድረ በዳ እንደሚመለከት ሕይወት እንዳለው ሰው አድርጎ ያቀርበዋል፡፡“ከምድረ በዳው ይልቅ ከፍ ያለ ነው”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:21

እሥራኤልም

እዚህ ላይ “እሥራኤል”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እሥራኤልን ሕዝብና በተለይም መሪዎቿን ነው፡፡“ከዚያ በኋላ እሥራኤላውያን”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ እርሻና ወይን ቦታ አንገባም

“በየትኛውም እርሻና የወይን ቦታችሁ አንገባም”

በንጉሥ ጎዳና

ይሄ ደማስቆን በስተ ሰሜንንና የአካብን ባህረ ሠላጤ በደቡብ በኩል የሚያስተሳስር አውራ ጎዳና ነው፡፡ይሄንን በዘኁልቁ 20፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በድንበራቸው ላይ ለማለፍ

“በእነርሱ ድንበር በኩል ለማለፍ” እዚህ ላይ “እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አሞራውያንን ነው፡፡

ያሃፅ

ይሄ የቦታ ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

እርሱም ከእሥራኤልም ጋር ተዋጋ

እዚህ ላይ “እርሱም”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ራሱንና ሠራዊቱን የሚወክለው ንጉሥ ሴዎን ነው፡፡“ከእሥራኤላውያን ጋር ተዋጉ”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:24

እሥራኤልም መታ

እዚህ ላይ “እሥራኤል” የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡“እሥራኤላውን ጥቃት አደረሱ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በሠይፍ ሥለት

“ስለታም በሆነው የሠይፉ ክፍል” “የሠይፍ ሥለት”የሚለው ቃል የሚያያዘው ከሞትና ፍፁም ከሆነ ጥፋት ጋር ነው፡፡“ሙሉ በሙሉ ድል ነሷቸው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የእነርሱን ምድር ወረሱ

“የአሞራውያንን ምድር ድል አደረጉ” እዚህ ላይ “የእነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው አሞራውያንን ነው፡፡

የአሞን ሕዝብ…አሞራውያን

“አሞናውያን..አሞራውያን”ወይም “አሞን ሕዝብ ወይም የአሞር ሕዝብ” እነዚህ ስሞች ተመሳሳይ ቢሆኑም የሚያመለክቱት ግን ሁለት የተለያዩ ሕዝቦችን ነው፡፡

የተመሸገ ነበረ

“ጠንካራ የሆነ መከላከያ ነበረው” እሥራአላውያን አሞናውያንን አላጠቁም፡፡

በሐሴቦንና በመንደሮቹ ሁሉ

እዚህ ላይ“ሁሉ”የሚለው ቃል አካታች ሲሆን የሐሴቦን ከተማ በቅርብ ካሉት መንደሮች ጋር ያለውን ግንኙነት ይገልፃል፡፡“ሐሴቦንና የሚቆጣጠራቸው በቅርብ የሚገኙ ከተሞች”

ሴዎን እርሱን ከተማዎች ሁሉ ወስዶ ነበር

እዚህ ላይ“የእርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የሞአብን ንጉሥ ነው፡፡

Numbers 21:27

ሐሴቦን … የሴዎን ከተማ

እነዚሀ የሚያመለክቱትለአንድ ከተማ የተሰጡ ሁለት ስሞችን ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የሴዎን ከተማ ይሰራ፤ይመሥረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንድ ሰው የሴዎንን ከተማ ይገንባና ይመሥርት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እንደገና ይገንባና ዳግም ይመሥርት

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ቃላት ተመሣሣይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ከተማዋ ሙሉ በመሉ የምትገነባ ስለመሆኗ አስረግጦ ለመናገር ነው፡“ሙሉ በሙሉ ዳግም ይገነባል”(ሁለት ተመሳሳይ የሆነ ገፅታ ያላቸው የሚለውን ይመልክቱ)

እሣት ከሐሴቦን፤ነበልባልም ከሴዎን ወጣ

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ቃላት ተመሣሣይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆንውድመቱ ከሐሴቦን እንደሚጀምር አስረግጦ ይናገራል፡፡እሣቱ የሚያመለክተው አጥፊ የሆነ ሠራዊትን ነው፡፡“ንጉሥ ሴዎን ከሐሴቦን ከተማ ጠንካራ የሆነ ጦርን እየመራ መጣ” (ተመሳሳይነት የሚለውንናምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የሞአብን ዔር፤የአርኖንን ተራራ አለቆች በላ

የሴዎን ሠራዊት የዔርን ከተማ እንደሚበላ አውሬ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“በሞአብ ምድር ያለውን የኤርን ከተማ አጠፋ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:29

ሞአብ…የኮሞስ ሕዝብ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች የሚያመለክቱት አንድ ዓይነት ሕዝብን ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የኮሞስ ሕዝብ

ኮሞስ ሞአባውያን ያመለኩት የነበረ ጣዖት ነው፡፡“ኮሞስን የሚያመልክ ሕዝብ”

የራሱ ልጆችን እርሱ ሰጠ

“እርሱ”እና “የራሱ”የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት ኮሞስን ነው፡፡

እኛ ድል አድርገናል

እዚህ ላይ “እኛ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ዲቦን ድል የነሱትን እሥራኤላውያንን ነው፡፡

ሐሴቦን ፈራርሷል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሐሴቦንን ደምስሰናታል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሐሴቦን…እስከ ዴቦን ድረስ…ከኖፋም አስከ ሜድባ ድረስ

እነዚህ ሁሉ በሴዎን መንግሥት ውስጥ የነበሩ ቦታዎች ናቸው፡፡ይሄ የሚያሳየው እሥራኤላውያን የሴዎንን አገር ሁሉ ሙሉ በሙሉ አጥፍተውታል ማለት ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ሆን ብሎ አጋኖ መናገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 21:31

አባረሩ

“አሳደዷቸው”

Numbers 21:33

በእነርሱ ላይ ወጡ

“አጠቋቸው”

በአሞራውያን ንጉሥ በሴዎን እንዳደረግህ እንዲሁ ታደርግበታለህ

እሥራኤላውያን ሴዎንን ፈፅመው አጥፍተዋት ነበር፡፡“የአሞራውያንን ንጉሥ ሴዎንን እንዳጠፋህ እንዲሁ አጥፋው”

ስለዚህ ገደሉት

“ስለዚህ የእሥራኤል ሠራዊት ዓግን ገደለው፡፡

ሰውም አልቀረለትም

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእርሱ የሆኑት ሰዎች ሁሉ ሞቱ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሩንም ወረሱ

“የእርሱን ምድር በቁጥጥራቸው ሥር አደረጉት”


Chapter 22

1 የእስራአል ህዝብ ከከተማዋ ከዮርዳኖስ ወንዝ ሌላ ዳርቻ ኢያሪኮ አጠገብ ወደሚገኘው የሞአብ ሜዳ ደርሰው እስኪሰፍሩ ደረስ ተጓዙ፡፡ 2 የሴፎር ልጅ ባላቅ እስራኤል በአሞራዊያን ላይ ያደረገውን ሁሉ አየ፡፡ 3 ሞአብ የእስራኤልን ህዝብ በጣም ፈርቶ ነበር ምክንያቱም ብዙ ነበሩ፣ እናም ሞአብ በእስራኤል ህዝብ ተሸብሮ ነበር፡፡ 4 የሞብ ንጉስ ለምድያም ሽማግሌዎች፣ “ይህ ብዙ ህዝብ፣ በሬ በሜዳ ላይ ያለን ሳር በልቶ እንደሚጨርስ በዙሪያችን ያለውን ሁሉ በልቶ ይጨርሳል፡፡” አለ፡፡ በዚያን ጊዜ የሴፎር ልጅ ባላቅ የሞዓብ ንጉስ ነበር፡፡ 5 እርሱም በአገሩና በወገኖቹ መሀል በኤፍራጦስ ወንዝ አጠገብ በፋቱራ ወደተቀመጠው የቢያር ልጅ በልዓም መልዕክተኞችን ላከ፡፡ አስጠርቶትም እንዲህ አለው፣ “እነሆ፣ ከግብጽ አንድ ህዝብ ወደዚህ መጥቷል፡፡ የምድርን ፊት ሸፍነዋል፣ ደግሞም እዚሁ አጠገቤ ናቸው፡፡ 6 ስለዚህ አሁን መጥተህ ይህን ህዝብ ርገምልኝ፣ ምክንያቱም ከእኔ አቅም በላይ ናቸው፡፡ ምናልባት ከረገምክልኝ በኋላ እነርሱን ለማጥቃትና ከምድሪቱ ለማባረር እችል ይሆናል፡፡ የባረከው ሁሉ እንደሚባረክ አውቃለሁ፣ የረገምከው ሁሉ እንደሚረገም አውቃለሁ፡፡” 7 ስለዚህ የሞአብ ሽማግሌዎችና የምድያም ሽማግሌዎች የምዋርቱን ዋጋ ይዘው ሄዱ፡፡ ወደ በለዓም መጥተው የባላቅን ቃል ነገሩት፡፡ 8 በለዓምም እንዲህ አላቸው፣ “ዛሬ ምሽት እዚህ እደሩ፡፡ ያህዌ የሚለኝን አሳውቃችኋለሁ፡፡” ስለዚህም የሞብ መሪዎች ያን ምሽት ከበለዓም ዘንድ ተቀመጡ፡፡ 9 እግዚአብሔር ወደ በለዓም መጥቶ እንዲህ አለው፣ “ወደ አንተ የመጡት እነዚህ ሰዎች እነማን ናቸው” 10 በለዓም ለእግዚአብሔር እንዲህ ሲል መለሰለት፣ “የሞአብ ንጉስ የሴፎር ልጅ ባላቅ፣ እነርሱን ወደ እኔ ልኳቸዋል፡፡ እንዲህም አለ፣ 11 ‘እነሆ፣ ከግብጽ የመጡ ሰዎች የምድሬን ገጽ ሸፍነዋል፡፡ አሁን መጥተህ እነርሱን ርገምልኝ፡፡ ይህ ከሆነ ምናልባት እነርሱን መዋጋትና ማባረር እችል ይሆናል፡፡” 12 እግዚአብሔር ለበለዓም እንዲህ መለሰለት፣ “ከእነዚህ ሰዎች ጋር መሄድ የለብህም፡፡ የእስራአልን ህዝብ መርገም የለብህም ምክንያቱም እነርሱ የተባረኩ ናቸው፡፡” 13 በለዓም በጠዋት ተነስቶ ለባላቅ መሪዎች እንዲህ አላቸው፣ “ወደ ምድራችሁ ተመልሳችሁ ሂዱ ምክንያቱም ያህዌ ከእናንተ ጋር እሄድ ዘንድ አልፈቀደልኝም፡፡ 14 ስለዚህም የሞብ መሪዎች ተመልሰው ወደ ባላቅ ሂዱ፡፡ እንደህም አሉት፣ “በለዓም ከእኛ ጋር ለመምጣት አልፈቀደም፡፡” 15 ባላቅ እንደገና ከመጀመሪያዎቹ መልዕክተኞች የከበሩ ብዙ መሪዎችን ላከ፡፡ 16 እነርሱም ወደ በለዓም መጥተው እንዲህ አሉት፣ “የሴፎር ልጅ ባላቅ እንዲህ ብሏል፣ ‘እባክህ ወደ እኔ ለመምጣት አንዳች ነገር አያግድህ፣ 17 ምክንያቱም እጅግ ከፍ ያለ ክፍያ እከፍልሃለሁ፣ ታላቅ ክብርም እሰጥሃለሁ፣ ደግሞም እንዳደርገው የምትነግረኝን ሁሉ አደርጋሁ፡፡ ስለዚህ እባክህ መጥተህ ይህን ህዝብ ርገምልኝ” 18 በለዓለም ለባላቅ ሰዎች እንዲህ ሲል መለሰላቸው፣ “ባላቅ ብርና ወርቅ የሞላበትን ቤተ መንግስቱን ቢሰጠኝ እንኳን ከአምላኬ፣ ከያህዌ ቃል አልፌ መሄድ አልችልም፣ ደግሞም እርሱ ከነገረኝ አሳንሼ ወይም ጨምሬ አላደርግም፡፡ 19 ስለዚህ አሁን፣ እባካችሁ ያህዌ የሚለኝን ተጨማሪ ነገር አውቅ ዘንድ ዛሬ ምሽትም ደግሞ በዚህ እደሩ፡፡” 20 እግዚአብሔር በምሽት ወደ በለዓም መጥቶ እንዲህ አለው፣ “እነዚህ ሰዎች ወደ አንተ እስከ መጡ ድረስ ተነስተህ ከእነርሱ ጋር ሂድ፡፡ ነገር ግን እንድታደርገው የምነግርህን ብቻ አድርግ፡፡” 21 በለዓም በጠዋት ተነስቶ አህያውን ጫንና ከሞአብ መሪዎች ጋር ሄደ፡፡ 22 ነገር ግን በመሄዱ፣ የእግዚአብሔር ቁጣ ነደደ፡፡ የያህዌ መልአክ፣ በአህያው ላይ ተቀምጦ የሚሄደውን በለዓምን ሊቃወመው በመንገድ ላይ ቆመ፡፡ የበለዓም ሁለቱ አገልጋዮቹም አብረውት ነበሩ፡፡ 23 አህያዋ የያህዌን መልአክ የተመዘዘ ሰይፉን ይዞ በመንገድ ላይ ቆሞ አየችው፡፡ አህያዋ ከመንገድ ዘወር ብላ ወደ ሜዳው ሄደች፡፡ በለዓለም አህያይቱን ወደ መንገድ እንድትለስ መታት፡፡ 24 የያህዌ መልአክ በመንገዱ ጠባብ መተላፊያ ላይ በወይን እርሻው መሀል፣ በስተቀኙና በስተግራው ግድግዳ ባለበት ስፍራ ቆመ፡፡ 25 አህያይቶ የያህዌን መልአክ አየች፡፡ ወደ ግድግዳው ተጠግታ የበለዓምን እግር አጣበቀችው፡፡ በለዓም እንደገና አህያይቱን መታት፡፡ 26 የያህዌ መልአክ እንደ ገና ራቅ ብሎ ሄዶ ወደ የትኛውም አቅጣጫ መዞሪያ በሌለበት ሌላ ጠባብ መተላፊያ ስፍራ ቆመ፡፡ 27 አህያይቱ የያህዌን መልአክ አይታ ከበለዓም በታች ተኛች፡፡ የበለዓም ቁጣ ነደደ፣ በበትሩም አህያይቱን መታት፡፡ 28 ያህዌ የአህያይቱን አፍ ስለከፈተ መናገር ቻለች፡፡ በለዓምን እንዲህ አለችው፣ “እነዚህን ሶስት ጊዜያት እንድትመታኝ የሚያደርግ ምን ነገር አደረግሁብህ” 29 በለዓም አህያይቱን፣ “በእኔ ላይ የማይረባ ድርጊት ስለፈጸምሽ ነው፡፡ በእጄ ላይ ሰይፍ ቢኖር እወድ ነበር፡፡ በእጄ ላይ ሰይፍ ቢኖር ኖሮ፣ ይህን ጊዜ ገድዬሽ ነበር” አላት፡፡ 30 አህያይቱ በለዓምን እንዲህ አለችው፣ “እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ ስትቀመጥብኝ የኖርክብኝ አህያህ አይደለሁምን? ከዚህ በፊት እንዲህ ያለ ነገር በአንተ ላይ የማድረግ ልማድ ነበረኝን?” በለዓም “እይ” አለ፡፡ 31 ከዚያ ያህዌ የበለዓምን ዐይኖች ከፈተ፣ እናም የያህዌ መልአክ በእጁ ሰይፉን ይዞ በመንገዱ ላይ ቆሞ አየ፡፡ በለዓም ዝቅ ብሎ በግምባሩ ተደፋ፡፡ 32 የእግዚአብሔር መልአክ እንዲህ አለው፣ “አህያህን ለምን በእዚህ ሶስት ጊዜያት መታሀት የምቃወምህ ሆኜ መጥቻለሁ ምክንያቱም ድርጊቶችህ በፊቴ መጥፎዎች ነበሩ፡፡ 33 አህያይቱ አይታኝ በእነዚህ ሶስት ጊዜያት ከእኔ ዞር አለች፡፡ እርሷ ዞር ባትልልኝ ኖሮ፣ በእርግጥ አንተን እገድልህና የእርሷን ነፍስ እተው ነበር፡፡” 34 በለዓም ለያህዌ መልአክ እንዲህ አለ፣ “እኔ በድያለሁ፡፡ እኔን ተቃውመህ በፊቴ ቆመህ እንደነበር አላወቅሁም፡፡ አሁን እንግዲህ፣ ይህ ጉዞ አንተን ደስ ካላሰኘ፣ ወደመጣሁበት እመለሳለሁ፡፡” 35 የያህዌ መልአክ ግን በለዓምን እንዲህ አለው፣ “ከሰዎቹ ጋር ጉዞህን ቀጥል፡፡ ነገር ግን እኔ የምነግርህን ብቻ መናገር አለብህ፡፡” ስለዚህም በለዓም ከባላቅ መሪዎች ጋር ሄደ፡፡ 36 ባላቅ የበለዓምን መምጣት ሲሰማ፣ ሞአብ ውስጥ ወዳለችው በድንበር ላይ ወደምትገኘው አርኖን ከተማ ሊቀበለው ወጣ፡፡ 37 ባላቅ በለዓምን እዲህ አለው፣ “እንዲጠሩህ ሰዎችን ወደ አንተ አልላኩም ነበርን? ለምን ወደ እኔ አልመጣህም? እኔ ላከብርህ አልችልምን?” 38 ከዚያም በለዓም ለባላቅ መለሰለት፣ “በእርግጥ ወደ አንተ መጥቻለሁ፡፤ አሁን አንዳች ነገር ለመናገር እኔ አንዳች ሀይል አለኝን? መናገር የምችለው እግዚአብሔር በአፌ ላይ ያስቀመጠውን ቃል ብቻ ነው፡፡” 39 በለዓም ከባላቅ ጋር ሄደ፣ እነርሱም ወደ ቂርያት ሐጾት ደረሱ፡፡ 40 ከዚያ ባላቅ በሬዎችንና በጎችን ሰዋ፣ ለበለዓምና ከእርሱ ጋር ለነበሩ መሪዎችም ሰጣቸው፡፡ 41 ማለዳ፣ ባላቅ በለዓምን ወደ ካሞት በኣል ይዞት ሄደ፡፡ በለዓም ከዚያ ሆኖ ማየት የሚችለው በሰፈሮቻቸው ካሉት እስኤላዊያን ጥቂቶቹን ብቻ ነበር፡፡



Numbers 22:1

በኢያሪኮ ፊት ለፊት በዮርዳኖስ ማዶ ባለው

እሥራኤላውያን የሰፈሩት ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተ ምሥራቅ በኩል ነበር፡፡ኢያሪኮ ደግሞ ከወንዙ በስተ ምዕራብ በኩል ነበር፡፡

Numbers 22:2

የሴፎር ልጅ ባላቅ

ባላቅ የሞአብ ንጉሥ ነበር፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ሴፎር

ሴፎር የባላቅ አባት ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ሞአብ ከሕዝቡ የተነሣ እጅግ ፈራ…ከእሥራኤልም ልጆች የተነሣ ደነገጠ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ ዓይነት ትርጉም ያላቸው ሲሆን ሞአብ ምን ያህል እንደፈራ አፅንዖት የሚሰጡ ናቸው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ሞአብ እጅግ ፈራ

እዚህ ላይ “ሞአብ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የሞአብን ሕዝብ ነው፡፡“ሞአባውያን በሙሉ ከፍተኛ የሆነ ፍርሃት ይዟቸው ነበረ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ምክኒያቱም ብዙ ስለነበሩ

“ምከኒያቱም በቁጥር ብዙዎች ነበሩ”

የሞአብም ንጉሥ የምድያምን ሽማግሌዎች እንዲሀ አላቸው

ሞአባውያንና ምድያማውያን የተለያዩ ሕዝቦች ቢሆኑም በዚያን ወቅት ምድያማውያን ይኖሩ የነበሩት በሞአብ ምድር ውስጥ ነበር፡፡

በሬ የለመለመውን ሣር እንደሚጨርስ ይህ ጭፍራ በዙሪያችን ያለውን ሁሉ ይጨርሳል

እሥራኤላውያን ጠላቶቻቸውን የሚያጠፉበትን መንገድ በመስክ ላይ ሣርን እንደሚበሉ በሬዎች ተደርገው ተገልፀዋል፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

በዚያን ወቅት የሴፎር ልጅ ባላቅ የሞአብ ንጉሥ ነበር

ይሄ ዋናውን ታሪክ ስለ ባላቅ የኋላ ታሪክ መረጃ ወደ መስጠት ያዞረዋል፡፡(የጀርባ ታሪከ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 22:5

መልክተኞችን ላከ

“ባላቅ መልዕክተኞችን ላከ”

ቢኦር

ይሄ የበለዓም አባት ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ፋቱራ

ይሄ የአንድ ከተማ ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የራሱ አገርና የራሱ ሕዝብ

“የበለዓም አገርና ሕዝብ”

ጠራው

“ባላቅ በለዓምን ጠራው”ባላቅ በቀጥታ ከበለዓም ጋር አልተነጋገረም፡፡ሆኖም ሃሣቡን ያስተላለፈው በላካቸው መልዕክተኞች አማካይነት ነው፡፡

የምድሩን ፊት ሁሉ ሸፈኑ

ይሄ ብዛታቸውን ለመገለፅ ተጋንኖ የቀረበ አነጋገር ነው፡፡“እጅግ ብዙዎች ናቸው”(የተጋነነ ንፅፅር እና አጠቃላይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የምድሪቱን ፊት

ይሄ የሚያመለክተው የምድርን ገፅ ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ላሳድዳቸው

“ላባርራቸው”

አንተ የመረቅኸው ምሩቅ የረገምኸውም ርጉም እንደሆነ አውቃለሁና

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰዎችን የመባረክም ሆነ የመርገም ኃይል እንዳለህ እኔ አውቃለሁ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 22:7

የምዋርቱን ዋጋ

“የምዋርቱን ዋጋ”የሚለው አሕፅሮተ ሥምበድርጊት መልከ ሊገለፅ ይችለላል፡፡“እሥራኤልን እንዲረግም ለበለዓም የሚከፈል ገንዘብ”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ በለዓምም መጡ

“ወደ በለዓምም ሄዱ”የሚለውን አባባል ልትመርጡ ትችሉ ይሆናል፡፡(መሄድና መምጣት የሚለውን ይመልከቱ)

የባላቅንም ቃል ነገሩት

“ከባላቅ የተላከውን መልዕከት ነገሩት”

ባላቅ

ይሄ የሰው ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

አመጣላችኋለሁ

የበለዓም መልዕክት ልክ አንድን ዕቃ ተሸክሞ እንደሚመጣ ዓይነት ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡“እነግራችኋለሁ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 22:9

እግዚአብሔርም ወደ በለዓም መጣ

“እግዚአብሔር ለበለዓም ተገለጠለት

እነዚህ በአንተ ዘንድ የመጡት ሰዎች እነማናቸው?

እግዚአብሔር ጥያቄውን ያነሳው በአዲስ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ውይይት ለመጀመር ነው፡፡ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ በመግለጫ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ወደ አንተ ስለመጡት ሰዎች ማንነት ንገረኝ” (አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ባላቅ..ሴፎር

እነዚህየሰው ሥሞችናቸው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ሕዝቡን ተመልከት…አሳድዳቸው

በለዓም ባላቅ ለእርሱ የላከውን መልዕክት መልሶ ይናገረዋል፡፡እነዚህን ሐረጎች በዘኁልቁ 22፡5-6 ያለውን ክፍል እንዴት እንደተረጎማችኋቸው ተመልከቱ፡፡

አሳድዳቸው

“አባርራቸው”

Numbers 22:12

የተባረከ ነውና

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የባረክኋቸው በመሆኑ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ባላቅ

ይሄ ሰው ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 22:15

ወደ በለዓምም መጡ

“ወደ በለዓምም ሄዱ”የሚለውን ልትመርጡ ትችሉ ይሆናል፡፡(መሄድና መምጣት የሚለውን ይመልከቱ)

ባላቅ

ይሄ ሰው ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ይሄ ሕዝብ

ይሄ ነጠላ ሥም እሥራኤላውያንንየሚያየውልክ እንደ አንድ የህዝብ ስብስብ ነው፡፡

Numbers 22:18

ባላቅ

ይሄ ሰው ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ባላቅ በቤቱ የሞላውን ወርቅና ብር ቢሰጠኝ

በለዓም ፈፅሞ ሊሆን የማይችል ነገርን እየገለፀ ነው፡፡እግዚአብሔርን እንዳይታዘዝ ሊያደርገው የሚችል ነገር ሊኖር እንደማይችል አስረግጦ እየተናገረ ነው፡፡(ተግባራዊ ሊሆኑ የማይችሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በትንሹ ወይም በትልቁ የአምላኬን የእግዚአብሔርን ቃል እተላለፍ ዘንድ አይቻለኝም

ይሄ የሚያሣየው በምንም ሁኔታ ውስጥ ቢሆን በለዓም እግዚአብሔርን ከመታዘዝ ወደ ኋላ የማይል መሆኑን ነው፡፡

Numbers 22:21

ኮርቻውን አህያው ላይ ጫነ

ኮርቻ እንስሳት ጀርባ ላይ ለግልቢያ ሲባል የሚደረግ መቀመጫ ነው፡፡

የእግዚአብሔርም ቁጣ ነደደ

የእግዚአብሔር ቁጣ የመጨመሩ ነገር ልክ እሣት መንደድ እንደሚጀምር ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በኃይል ተቆጣ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በበለዓም ላይ ጥላቻ እንዳለው ሰው

“እንደ በለዓም ጠላት” ወይም “በለዓምን ለማስቆም”

የተመዘዘም ሠይፍ

ሠይፍ ጥቅም ላይ ሊውል ከሰገባው ወጥቷል፡፡“ጥቃት ለማድረስ ሠይፉን ዝግጁ አደረገ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አህያይቱም ከመንገድ ፈቀቅ ብላ ወደ እርሻው ውስጥ ገባች

አህያይቱ ይህንን ያደረገችው ከእግዚአብሔር መልአክ ለመሸሽ ብላ ነው፡፡

እርሷን ይመልሳት ዘንድ

አንዳንድ ጊዜ እንስሳት“የእርሷ”ወይም “እርሷ”በመባል ይጠቀሳሉ፡፡“ሊመልሰው”

Numbers 22:24

ወደ ቅጥሩ ተጠጋች

ይሄ ሙከራ በመንገድ ላይ ቆሞ ከነበረው መልአክ ለማምለጥ የተደረገ ነው፡፡

እርሷ ሄደች

አንዳንድ ጊዜ እንስሳት“የእርሷ”ወይም “እርሷ”በመባል ይጠቀሳሉ፡፡“ሄደ”

የበለዓምን እግር ከቅጥሩ ጋር አጣበቀች

“የበለዓምን እግር ከቅጥሩ ጋር አጋጨችው”ወይም “የበለዓምን እግር ከቅጥሩ ጋር ስታጣብቀው እግሩ ተጎዳ”

Numbers 22:26

በለዓምም እጅግ ተቆጣ

የበለዓም ቁጣ የመጨመሩ ነገር ልክ እሣት መንደድ እንደሚጀምር ዓይነት ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡በዘኁልቁ 22፡22 ላይ ያለውን ተመሳሳይ ሐረግ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“በለዓም በኃይል ተናደደ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 22:28

እግዚአብሔርም የአህያይቱን አፍ ከፈተ

የመናገር ችሎታ አፍ ከመክፈት ጋር ተነፃፅሯል፡፡“ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር ልክ እንደ ሰው እንደሚናገር ለአህያይቱ የመናገር ችሎታን ሰጣት”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

በለዓምን ተናገረችው

“አህያይቱ በለዓምን ተናገረችው”

ከብዙ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ የምትቀመጥብኝ አህያህ አይደለሁምን?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የተጠየቀበት ምክኒያት በለዓም በአህያዋ ላይ የሰራው ጥፋት ተገቢነት የሌለው መሆኑን ለመግለፅ ነው፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ከብዙ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ የምትቀመጥብኝ አህያህ ነኝ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በውኑ እንዲህ አደርግ ዘንድ ልማዴ ነውን?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የተጠየቀበት ምክኒያት በለዓም በአህያዋ ላይ የሰራው ጥፋት ተገቢነት የሌለው መሆኑን ለመግለፅ ነው፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለአንተ እንደዚህ ዓይነት ባህርይ የማሳየት ልማድ አልነበረኝም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 22:31

እግዚአብሔርም የበለዓምን ዓይኖች ከፈተ፤የእግዚአብሔርንም መልአክ አየ

የአንድ ሰው“ዓይን መክፈት” “ከማየት ችሎታ”ጋር ተነፃፅሮ ቀርቧል፡፡“ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር ለበለዓም የማየት ችሎታን ሰጠው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የተመዘዘም ሠይፍ ይዞ

ሠይፍ ጥቅም ላይ ሊውል ከሰገባው ወጥቷል፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡23 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ለማጥቃት ከተዘጋጀ ሠይፉ ጋር”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በለዓም ሰገደ፤በግንባሩም ወደቀ

ይሄ የሚያሣየው በዓለም ራሱን በመልአኩ ፊት ማዋረዱን ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

አህያህን ሦስት ጊዜ ለምን መታህ?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የተነሳበት ምክኒያት በለዓም የሰራው ሥራ ጥፋት መሆኑን ለማሳሰብ ነው፡፡ይሄ በመገለጫ መልክ ሊተረጎም ይችለል፡፡“አህያህን ሦስት ጊዜ መምታት አልነበረብህም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ጥላቻ እንዳለው ሰው

“ጠላትህ እንደሆነ ሰው” ወይም “ተቃዋሚምህ እንደሆነ ሰው”

ከፊቴ ፈቀቅ ባላለች በእውነት አንተን በገደልሁህ እርስዋንም ባዳንኋት ነበር

ይሄ ግምታዊ አባባል የሚያሣየው ሊከሰት ይችል የነበረን ነገርና ከአህያይቱ ድርጊት የተነሣ የበለዓም ሕይወት መትረፉን ነው፡፡(በግምት ላይ የተመሰረቱ ሁኔታዎች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 22:34

አሁን አትወድድ እንደሆነ

“ጉዞዬን እንድቀጥል የማትፈልግ ከሆነ”

ከባላቅ አለቆች ጋር

“ባላቅ ከላካቸው አለቆች ጋር” “ባላቅን” በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 22:36

አርኖን

ይሄ የወንዝ ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 21፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በውኑ አንተን ለመጥራት አልላኩህብምን?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የተጠየቀው በለዓም በመዘግየቱ ምክኒያት ለመገሰፅ ነበር፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊረጎም ይችላል፡፡“በእርግጥ ሰዎች እንዲጠሩህ ልኬብህ ነበር” (ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ለምንስ ወደ እኔ አልመጣህም?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የተጠየቀው በለዓም በመዘግየቱ ምክኒያት ለመገሰፅ ነበር፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊረጎም ይችላል፡፡“ወደ እኔ መምጣት ነበረብህ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በውኑ እኔ አንተን ማክበር አልችልምን?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የተጠየቀው በለዓም በመዘግየቱ ምክኒያት ለመገሰፅ ነበር፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊረጎም ይችላል፡፡“በእርግጥም ወደ እኔ ዘንድ በመምጣትህ ገንዘብ ልከፍልህ እንደምችል አንተ ታውቃለህ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 22:38

በውኑ አንዳች ነገር እናገር ዝንድ እችላለሁን?

በለዓም ይሄንን ጥያቄ የሚጠይቅበት አቢይ ምክኒያት ባላቅ እንዲያደርግ የሚፈልገውን ነገርሁሉ ለማድረግ የማይችል መሆኑን ለመናገር ነው፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊረጎም ይችላል፡፡“ነገር ግን የምፈልገውን ነገር ሁሉ የመናገር ሥልጣን የለኝም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር በአፌ የሚያስቀምጠውን ቃል እርሱን እናገራለሁ

ይሄ መልዕክት የሚነገረው ልክ አንድን ነገር እግዚአብሔር በአፉ ውስጥ እንደሚያስቀምጥ ዓይነት ተደርጎ ነው፡፡“እግዚአብሔር እንድናገረው የሚፈልገው መልዕክት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ቂርያት ሐፆት

ይሄ የከተማ ሥም ነው፡፡

ጥቂት ሥጋ

“ከመሥዋዕቱ ጥቂት ሥጋ”

Numbers 22:41

ወደ በአል ኮረብታ

ይህንን ሃሣብ ሊገልፁ የሚችሉት 1/ይሄ በዘኁልቁ 29፡11 ላይ ካለው የማሞዝሥፍራን ያመለክታል፡፡ማሞዝ የሚለው ቃል ከፍታ የሆነ ሥፍራ ማለት ነው፡፡ወይም 2/ሰዎች ለበአል መሥዋዕት የሚያቀርቡበት ሌላ ሥፍራ ነው፡፡


Chapter 23

1 በለዓም ባላቅን እንዲህ አለው፣ “በዚህ ሰባት መሰዊያዎችንና ሰባት በሬዎችን እንዲሁም ሰባት አውራ በጎችን አዘጋጅልኝ፡፡” 2 ስለዚህም ባላቅ በለዓም እንደጠየቀው አደረገ፡፡ ከዚያም ባላቅና በለዓም በእያንዳንዱ መሰዊያ ላይ አንድ በሬና አንድ አውራ በግ አቀረቡ፡፡ 3 ከዚያ በለዓም ባላቅን እንዲህ አለው፣ “አንተ በሚቃጠል መስዋዕትህ አጠገብ ቁም እኔ እሄዳለሁ፡፡ ምናልባት ያህዌ ሊገናኘኝ ይመጣ ይሆናል፡፡ እርሱ የሚያሳየኝን ሁሉ እነግርሀለሁ፡፡” ስለዚህም በለዓም ዛፎች ወደ ሌሉበት የተራራ ጫፍ ሄደ፡፡ 4 እግዚአብሔር እርሱን ተገናኘው፣ በለዓምም ለእግዚአብሔር እንዲህ አለ፣ “እኔ ሰባት መሰዊያዎችን አበጅቻለሁ፣ ደግሞም በእያንዳንዱ ላይ አንድ በሬና አንድ አውራ በግ አቅርቤያለሁ፡፡” 5 ያህዌ በበለዓም አፍ ላይ መልዕክት አኑሮ እንዲህ አለ፣ “ወደ ባላቅ ተመለስና እንዲህ በለው፡፡” 6 ስለዚህ በለዓም በሚቃጠል መስዋዕቱ አጠገብ ወደቆመው ወደ ባላቅ ከእነርሱ ጋር ወደ ነበሩት የሞአብ መሪዎች ሁሉ ተመለሰ፡፡ 7 ከዚያ በለዓም ትንቢቱን መናገር ጀመረ እንዲህም አለ፣ “ባላቅ እኔን ከአራም አመጣኝ፣ የሞአብ ንጉስ ከምስራቅ ተራሮች አመጣኝ፡፡ ‘ና፣ ያዕቆብን ዕርገምልኝ’ አለኝ፡፡ ‘ና፣ እስራኤልን ተፈታተንልኝ’ አለኝ፡፡ 8 እግዚአብሔር ያልረገመውን እኔ እንዴት መርገም እችላለሁ? ያህዌ ያልተቃወማቸውን እኔ እንዴት መቃወም እችላለሁ? 9 ከአለቶች በላይ ሆኜ አየዋለሁ፣ ከተራሮች ላይ ሆኜ ወደ እርሱ አያለሁ፡፡ ተመልከት፣ ብቻውን የሚኖር ራሱን እንደ ተራ ህዝብ አድርጎ የማይቆጥር ህዝብ አለ፡፡ 10 የያዕቆብን ትቢያ ማን መቁጠር ይችላል ወይም ከእስራኤል ሩቡን እንኳን ማን ይቆጥራል? የጻድቁነ ሞት እኔ ልሙት፣ ደግሞም የህይወቴ መጨረሻ እንደ እርሱ ይሁን!” 11 ባላቅ በለዓምን እንዲህ አለው፣ “ምን እያደረግክብኝ ነው ጠላቶቼን እንድትረግምልኝ አመጣሁህ፣ ነገር ግን እነሆ አንተ እነርሱን ባረካቸው፡፡” 12 በለዓም መለሰለት እንዲህም አለ፣ “ያህዌ በአፌ ላይ ያደረገውን ብቻ ለመናገር መጠንቀቅ የለብኝምን?” 13 ስለዚህም ባላቅ እንዲህ አለው፣ “እባክህ ከእኔ ጋር ልታያቸው ወደ ምትችልበት ሌላ ቦታ ና፡፡ ከእነርሱ ሁሉንም ሳይሆን፣ በቅርብ ያሉትን ብቻ ታያለህ፡፡ በዚያ እነርሱን ትረግምልኛለህ፡፡” 14 ስለዚህ በለዓምን ወደ ጾፊም ሜዳ፣ ወደ ፊስጋ ተራራ ጫፍ ይዞት ሄደና ተጨማሪ ሰባት መሰዊያዎችን አበጀ፡፡ በእያንዳንዱ መሰዊያ አንድ በሬና አንድ አውራ ጠቦት ሰዋ፡፡ 15 ከዚያ በለዓም ባላቅን እንዲህ አለው፣ “እኔ በዚያ ያህዌን ለመገናኘት ስሄድ፣ አንተ እዚህ በሚቃጠል መስዋዕትህ አጠገብ ቁም፡፡” 16 ያህዌ በለዓምን ተገናኝቶ በአፉ ምልክት አኖረ፡፡ እንዲህም አለው፣ “ወደ ባላቅ ተመለስና መልዕክቴን ንገረው፡፡” 17 በለዓም ወደ ባላቅ ተመልሶ በሚቃጠል መስዋዕቱ አጠገብ አገኘው፣ የሞአብ መሪዎችም ከእርሱ ጋር ነበሩ፡፡ ባላቅ እንዲህ ሲል ጠየቅ፣ “ያህዌ ምን ነገረህ?” 18 በለዓም ትንቢቱን መናገር ጀመረ፡፡ እንዲህም አለ፣ “ባላቅ፣ ተነስና አድምጥ፡፡ አንተ የሴፎር ልጅ እኔን አድምጠኝ፡፡ 19 እግዚአብሔር ይዋሽ ዘንድ ሰው አይደለም፣ ወይም ሀሳቡን ይቀየር ዘንድ የሰው ልጅ አይደለም፡፡ ላያደርግ አንዳች ነገር ቃል ይገባልን? ላይፈጽመውስ አንዳች ነገር አደርጋለሁ ይላልን? 20 እነሆ፣ ለመባረክ ታዝዣለሁ፡፡ እግዚአብሔር በረከትን ለቋል፣ እኔ ልከለክል አልችልም፡፡ 21 እርሱ በያዕቆብ ላይ አንዳች ችግር ወይም በእስራኤል ላይ ድካም አላየም፡፡ ያህዌ አምላካቸው ከእነርሱ ጋር ነው፣ የንጉሳቸውም እልልታ ከእነርሱ ጋር ነው፡፡ 22 እግዚአብሔር እንደ ጎሽ በሆነ ሀይል ከግብጽ አወጣቸው፡፡ 23 በያዕቆብ ላይ የሚሰራ ምንም አስማት የለም፣ የትኛውም ሟርት እስራኤልን አይጎዳም፡፡ ይልቁንም ስለያዕቆብና ስለ እስራኤል እንዲህ ይባልላቸዋል፣ ‘እግዚአብሔር ያደረገውን እዩ!’ 24 እዩ፣ ህዝቡ እንደ እንስት አንበሳ ይነሳል፣ እንደ አንበሳ ተነስቶ ያጠቃል፡፡ ያደነውን እስኪበላ የገደለውን ደም እስኪጠጣ አያርፍም፡፡” 25 ከዚያ ባላቅ በለዓምን እንዲህ አለው፣ “እነርሱን ባትረግማቸው እንኳን ጨርሰህ አትባርካቸው፡፡” 26 በልዓም ግን ባላቅን መልሶ እንዲህ አለው፣ “እንድናገር ያህዌ የነገረኝን ሁሉ መናገር እንዳለብኝ አልነገርኩህምን?” 27 ስለዚህም ባላቅ ለበለዓም እንዲህ ሲል መለሰለት፣ “አሁን ና፣ እኔ ወደ ሌላ ስፍራ እወስድሃለሁ፡፡ ምናልባት በዚያ እነርሱን እንድትረግምልኝ እግዚአብሔር ይፈቅድልህ ይሆናል፡፡” 28 ስለዚህም ባላቅ በለዓምን ምድረበዳውን ቁልቁል ወደሚያይበት ወደ ፌጎር ተራራ ጫፍ ወሰደው፡፡ 29 በለዓም ባላቅን እንዲህ አለው፣ “በዚህ ስፍራ ሰባት መሰዊያዎችን አብጅና ሰባት በሬዎች እንዲሁም ሰባት አውራ በጎች አዘጋጅ፡፡” 30 ስለዚህ ባላቅ ባለዓም እንደነገረው አደረገ፤ በእያንዳንዱ መሰዊያ ላይ አንድ በሬና አንድ አውራ በግ ሰዋ፡፡



Numbers 23:1

ባላቅ

ይሄ የሞአብ ንጉሥ ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ሰባትም ወይፈን ሰባትም አውራ በግ በዚህ አዘጋጅልኝ

“ሰባትም ወይፈን ሰባትም አውራ በግ ለመሥዋዕት እረድልኝ”

በመሥዋትህ ዘንድ ቆይ እኔም እሄዳለሁ

“በዚህ በመሥዋትህ ዘንድ ቆይ እኔም ራቅ ወዳለ ሥፍራ እሄዳለሁ”

Numbers 23:4

አንድ ወይፈንና አንድ አውራ በግ አሳርጌያለሁ

እነዚህን አንስሳት እንደሚቃጠል መሥዋዕት አድርጎ ስለማቅረቡ ቀደም ብሎ ተገልጿል፡፡“አንድ ወይፈንና አንድ በግ አዘጋጅቼ በመሥዋዕት መልክ አቃጥያቸዋለሁ” (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርም ቃልን በበለዓም አፍ አደረገ

እግዚአብሔር በለዓም እንዲናገር የሚሰጠውን መልዕክት ልክ በአፉ እንደሚያስቀምጠው ዓይነት ተደርጎ ተነግሯል፡፡“እግዚአብሔር ለባላቅ መነገር የሚገባውን ነገር እንዲነግረው ለበለዓም ነገረው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:7

ባላቅ ከአራም አመጣኝ …የሞአብምንጉሥ ከምሥራቅ ተራሮች

እነዚህ ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ና ያዕቆብን እርገምልኝ …ና እሥራኤልን ተጣላልኝ ብሎ

እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮችተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡በለዓም የእሥራኤልን ሕዝብ እንዲረግም ጫና የሚያደርጉ ናቸው፡፡ (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ያልረገመውን እንዴት እረግማለሁ?እግዚአብሔር ያልተቃወመውን እንዴት እቃወማለሁ?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ በለዓም እግዚአብሔርን አልታዘዝም ለማለት ፈቃደኛ አለመሆኑን ያሣያል፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊተረጎም ይችላል፡፡“ነገር ግን እግዚአብሔር ያልረገመውን ልረግም አልችልም፡፡እግዚአብሔር ያልተጣላውን ልጣላ አልችልም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:9

በአምቦች ራስ ላይ ሆኜ አየዋለሁ…በኮረብቶችም ላይ ሆኜ እመለከተዋለሁ

እነዚህ ሁለት ሐረጎችተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡በለዓምከኮረብታ አናት ላይ ሆኖ እሥራኤልን ተመለከተ፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

እርሱን አየዋለሁ..እመለከተዋለሁ

እዚህ ላይ“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እሥራኤልን ነው፡፡

ሕዝብ አለ

“የተወሰነ የሕዝብ ክፍል አለ”

በአህዛብም መካከል አይቆጠርም

ይሄ አሉታዊ አነጋገር ጥቅም ላይ የዋለው ተቃራኒው ነገር እውነት መሆኑን አስረግጦ ለመናገር ነው፡፡“ራሣቸውን የተለየ ሕዝብ አድርገው ይቆጥራሉ”(በተዘዋዋሪ መንገድ ሃሣብን መግለፅ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:10

የያዕቆብን ትቢያ ማን ይቆጥራል?የእሥራኤልንስ እርቦ ማን ይቆጠራል?

“የያዕቆብ ትቢያ”ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን የእሥራኤል ሕዝብ ቁጥር የትቢያን ያህል ብዛት እንዳለው አድርጎ ይናገራል፡፡ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ በዓረፍተ ነገር መልክ ሊተረጎም ይችላል፡፡“ለቁጥር የሚያዳግቱ እሥራኤላውያን አሉ፡፡ብዙ ከመሆናቸው የተነሣ አንድ አራተኛውን እንኳን መቁጠር የሚችል ሰው አይኖርም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውንና ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የፃድቅ ሰው ሞት

ይሄ ሰላማዊ የሆነ ሞት እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ይሄ በዚህ መልክም ሊነገርም ይችላል፡፡“ሠላም የሞላበት የፃድቅ ሰው ሞት”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ፃድቅ ሰው … እንደ እርሱ

ይሄ የእሥራኤልን ሕዝብ እንደ አንድ ሰው አድርጎ የሚያመለክት ገላጭ ነው፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:11

ባላቅ

ይሄ የሞአብ ንጉሥ ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ያደረገህብኝ ምንድነው?

ባላቅ ይህንን ጥያቄ የጠየቀው በለዓምን ለመውቀስ ነበር፡፡ይሄንን ጥያቄ በዓረፍተ ነገር መልክም መተርጎም ይቻላል፡፡“ይህንን በእኔ ላይ አድረገሃል ብዬ አላምንም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ተመልከት

ይሄ የሚያመለክተው የሚመጣውን አስደንጋጭ ድርጊት ነው፡፡

እግዚአብሔር በአፌ ያደረገውን እናገር ዘንድ አልጠነቀቅምን?

በለዓም ይሄንን አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የሚጠይቀው ለድርጊቶቹ ምክኒያት ለመሥጠት ነው፡፡ይሄ በመግለጫ መልክ ሊተረጎም ይችላል፡“እግዚአብሔር የተናገረኝን ነገር ብቻ ለመናገር መጠንቀቅ አለብኝ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር በአፌ ያስቀመጠውን ነገር ብቻ እናገር ዘንድ

መልዕክቱ እገዚአብሔር በአፍ ውሰጥ እንደሚያስቀምጠው ዓይነት ነገር ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡ይህንንተመሳሳይ ሐረግ በዘኁልቁ 22፡38 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“እግዚአብሔር የሚናገረኝን ብቻ ለመናገር”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:13

እዚያ ሆነህ እርገምልኝ

“እዚያ ሆነህ እሥራኤላውያንን ትረግምልኛለህ”

ወደ ፆፊምም ሜዳ

“ፆፊም”የሚለው ቃል “አጥብቆ በዓይን መከታተል”ወይም “መሰለል” የሚገልፅ የግርጌ ማሰታወሻ ላይ ተርጓሚዎቹ ማስቀመጥ ሊኖርባቸው ይችል ይሆናል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የፈስጋ ተራራ

ይሄ የተራራ ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 21፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:16

ቃልንም በአፉ አደረገ

ይሄ መልዕክት ልክ እግዚአብሔር በአፉ ውስጥ እንዳደረገለት ዓይነት ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡ተመሰሳዩን ሐረግ በዘኁልቁ 22፡38 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“መናገር ያለበትን ነገር ነገረው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እንዲህም አለ

“ከዚያ እግዚአብሔር ተናገረ”

ባላቅ ሆይ ስማ…የሴፎር ልጅ ሆይ እድምጠኝ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን የተደጋገሙበት ምክኒያት ባላቅ ለጉዳዩ ትኩረት መሥጠት እንደሚኖርበት አፅንዖት ለመሥጠት ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የሴፎር ልጅ

ይሄ የሚያመለክተው ባላቅን ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 23:19

እርሱ ያለውን አያደርገውምን?የተናገረውንስ አይፈፅመውምን?

እነዚህ ሁለት ጥያቄዎች ተመሳሳይ ሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን እግዚአብሔር የተናገረውን ነገር የሚፈፅም ስለመሆኑ አፅንዖት ይሰጣሉ፡፡እነዚህ ሁለት አስፈላጊ የሆኑ ጥያቄዎቸ በዓረፍተ ነገር መልከ ሊገለፁ ይችላሉ፡፡“ቃል የገባውን ነገር ተግባራዊ ሳያደርግ የቀረበት ጊዜ የለም፡፡ምን ጊዜም ቢሆን አደርገዋለሁ ያለውን ነገር በትክክል ተግባራዊ ያደርገዋል”(ተመሳሳይነት የሚለውንና ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ለመባረክ ትዕዛዝን ተቀብያለሁ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር እሥራኤላውያንን እንድባርክ አዝዞኛል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:21

በያዕቆብ ላይ ክፋትን….በእሥራኤልም ላይ ጠማማነትን

እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት1/እግዚአብሔር ለእሥራኤል የሰጠው መልካም የሆኑ ነገሮችን ብቻ ነው፡፡ወይም2/በእነርሱ ላይ ፍርድን ያመጣ ዘንድ በእሥራኤል ላይ ምንም ዓይነት ኃጢአት አላየም፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የንጉሥም እልልታ በመካከላቸው አለ

“እግዚአብሔር ንጉሣቸው በመሆኑ በደስታ እልል ይላሉ”

ጉልበቱ አንድ ቀንድ እንዳለው በሬ ነው

ይሄ ንፅፅር የእግዚአብሔር ኃያል ጉልበት ከበሬ ጋር የሚነፃፀር መሆኑን ነው የሚያመለክተው፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:23

በያዕቆብ ላይ አስማት የለም …በእሥራኤልም ላይ ምዋርት የለም

እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ተመሣሣይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ማንም ሰው በእሥራኤል ላይ መርገምን ቢደርገ ሊሰራለት አይችልም ለማለት ነው፡፡“እዚህ ላይ ያዕቆብ የሚል ቃል የሚያመለክተው እሥራኤልን ነው” (ተመሳሳይነት የሚለውንና ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ይባላል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰዎች ሊናገሩ ይችሉ ይሆናል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ያደረገውን ተመልከቱ

እግዚአብሔር ለእነርሱ ያደረገላቸው ነገር መልካም መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡“እግዚአብሔር ለእነርሱ ያደረገላቸውን መልካም ነገር ተመልክቱ!”

Numbers 23:24

እነሆ ሕዝቡ እንደ እንሥት አንበሳ ይነሳል…ይገድላል

ይህ ጥቅስ ረዥም የሆነ ምሣሌያዊ አነጋገር ሲሆን እሥራኤል ጠላቷን ድል የማድረጓን ጉዳይ ልክ አንበሣ ያደነውን ነገር እንደሚበላ ዓይነት አድርጎ ያቀርበዋል፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:25

ባላቅ

ይሄ የሞአብ ንጉሥ ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

እግዚአብሔር የተናገረውን ነገር ሁሉ አደርጋለሁ ብዬ አልተናገርሁህምን?

በለዓም ይህንን እጅግ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ የሚጠይቀው ወደ ባላቅ ከመምጣቱ በፊትም ቢሆን እግዚአብሔርን ላለመታዘዝ ፈቃደኛ እንዳልሆነ ለባላቅ ማሳሰቢያን ለመሥጠት ነው፡፡ይሄ በዓረፍተ ነገር መልክ ሊተረጎም ይችላል፡፡“ከዚያ በፊት እግዚአብሔር የሚናገረኝን ነገር ብቻ እንደምናገር ነግሬሃለሁ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 23:28

ምድረ በዳውን ከላይ ወደሚመለከተው

ይሄ ምድረ በዳ እሥራኤል ሰፍሮበት የነበረው ሥፍራ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡“እሥራኤል በነበረበት ምድረ በዳውን ከላይ ወደሚመለከተው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 24

1 በለዓምም ያህዌ እስራኤልን መባረክ እንደፈቀደ ባየ ጊዜ፣ በሌላ ጊዜ እንደሚያደርገው አስማት ለማድረግ አልወጣም፡፡ ይልቁንም፣ ወደ ምድረበዳው ቁልቁል ተመለከተ፡፡ 2 ዐይኖቹን አቅንቶ እስራኤልን በየነገዱ ሰፍሮ አየ፣ የእግዚአብሔር መንፈስም በእርሱ ላይ መጣ፡፡ 3 ይህን ትንቢት ተቀብሎ እንዲህ ሲል ተናገረ፣ “ዐይኖቹ እጅግ የተከፈቱለት የቢዖር ልጅ በለዓም እዲህ ይላል፡፡ 4 እርሱ የእግዚአብሔርን ቃላት ይናገራል ይሰማልም፡፡ እርሱ ሁሉን ቻይ ከሆነው ዘንድ ዐይኖቹ ተከፍተውለት በፊቱ ከሚሰግድለት ዘንድ የሆነውን ራእይን ይመለከታል፡፡ 5 ያዕቆብ ሆይ ድንኳኖችህ ምንኛ ያማሩ ናቸው፣ እስራኤል ሆይ መኖሪያዎችህ እንዴት ያምራሉ! 6 እንደ ሸለቆዎች ተዘርግተዋል፣ በወንዝ ዳር እንዳሉ መናፈሻ ስፍራዎች፣ በያህዌ እንደተተከሉ ሬቶች፣ በውሃ ዳርቻ እንዳሉ ዝግባዎች ናቸው፡፡ 7 ማድጋዎቻቸው በውሃ የተትረፈረፉ ናቸው፣ ሰብላቸው ውሃ አይታጣውም፡፡ ንጉሳቸው ከአጋግ ይበልጣል፣ መንግስታቸው የከበረ ነው፡፡ 8 እግዚአብሔር እርሱን ከግብጽ አውጥቶታል፡፡ እንደ ጎሽ ብርታት አለው፡፡ የሚዋጉትን መንግስታት ይፈጃቸዋል፡፡ አጥንቶቻቸውን ይሰባብራል፡፡ በቀስቶቹ ይወጋቸዋል፡፡ 9 እንደ አንበሳ ይሰባብራቸዋል፣ እንደ ሴት አንበሳ ያደቃቸዋል፡፡ ማን ሊቋቋመው ይችላል? የሚባርኩት ሁሉ ይባረኩ፤ የሚረግሙት ሁሉ የተረገሙ ይሁኑ፡፡” 10 የባላቅ ቁጣ በበለዓም ላይ ነደደ፣ እጆቹን አጣፍቶ በለዓምን እንዲህ አለው፣ “እኔ ጠላቶቼን እንድትረግምልኝ ጠራሁህ፣ ነገር ግን አንተ ሶስት ጊዜም ባረካቸው፡፡ 11 ስለዚህ አሁኑኑ ከእኔ ተለይተህ ወደ ቤትህ ሂድልኝ፡፡ እጅግ አድርጌ አከብርሃለሁ ብዬ ነበር፣ ነገር ግን አንዳች ሽልማት እንዳታገኝ ያህዌ ከለከለህ፡፡” 12 ከዚያ በለዓም ለባላቅ እንዲህ ሲል መለሰለት፣ “ወደ እኔ ለላካቸው መልዕክተኞች እንዲህ ብያቸው ነበር፣ 13 ‘ባላቅ በብርና ወርቅ የተሞላውን ቤተ መንግስቱን ቢሰጠኝ እንኳን፣ ያህዌ ከተናገረው ውጭ አንዳች መጥፎ ወይም መልካም፣ ወይም አንዳች እኔ ላደርግ የምፈልገውን አልናገርም፡፡ መናገር የምችለው ያህዌ ተናገር ያለንን ብቻ ነው፡፡’ ይህን ለእነርሱ አልተናገርኩምን? 14 ስለዚህ እነሆ አሁን ወደ ህዝቤ እመለሳለሁ፡፡ ነገር ግን አሁን በቅድሚያ ይህ ህዝብ በሚመጡት ቀናት በአንተ ህዝብ ላይ ሊያደርግ ያለውን ላስጠንቅህ፡፡” 15 በለዓም ይህን ትንቢት መናገር ጀመረ፣ “ዐይኖቹ እጅግ የተከፈቱለት የቢዖር ልጅ በልዓም ይህን ናገራል፡፡ 16 ይህ ከእግዚአብሔር ዘንድ ቃል የሚሰማ ሰው ትንቢት ነው፣ ከልዑል ዘንድ ዕውቀት ከተሰጠው፣ ሁሉን ቻይ ከሆነው አምላክ ራዕይ ከተቀበለው፣ በተከፈተ ዐይን በፊቱ ከሚሰግደው፣ ሰው የተነገረ ትንቢት ነው፡፡ 17 እኔ እርሱን አያለሁ፣ ነገር ግን እርሱ አሁን እዚህ አይደለም፡፡ እኔ እርሱን እመለከታለሁ፣ ነገር ግን እርሱ በቅርብ አይደለም፡፡ ኮከብ ከያዕቆብ ይወጣል፣ በትረ መንግስት ከእስራኤል ይነሳል፡፡ እርሱ የሞአብን መሪዎችን ይበታትናል፣ የሴትንም ትውልዶች ያጠፋል፡፡ 18 ከዚያ እስራኤል በሃይል ድል የሚነሳው ኤዶም፤ የእስራኤል ርስት ይሆናል፣ ደግሞም የእስራኤል ጠላት የሆነው ሴይር፣ የእነርሱ ርስት ይሆናል፣ 19 ከያዕቆብ ግዛት ያለው ንጉስ ይወጣል፣ እርሱም ከከተማቸው የተረፉትን ቅሬታዎች ያጠፋል፡፡” 20 ከዚያ በለዓም አማሌቅን ተመልክቶ ትንቢት መናገር ጀመረ፡፡ እንዲህም አለ፣ “አማሌቅ ታላቅ ህዝብ ነበር፣ነገር ግን መጨረሻው ጥፋት ይሆናል፡፡” 21 ከዚያ በለዓም ወደ ቄናውያን ተመልክቶ ትንቢቱን ጀመረ፡፡ እንዲህም አለ፣ “የምትኖርበት ስፍራ አስተማማኝ ነው፣ ጎጆችህም በአለቶች መሀል ነው፡፡ 22 ሆኖም ግን እናንተ ቄናውያን አሶር ምርኮ አድርጎ ሲወስዳችሁ ትደመሰሳላችሁ፡፡” 23 ከዚያ በለዓም የመጨረሻውን ትንቢቱን መናገር ጀመረ፡፡ እንዲህም አለ፣ “አወይ! እግዚአብሔር ይህን ሲያደርግ ማን ይተርፋል? 24 መርከቦች ከኪቲም ዳርቻዎች ይመጣሉ፤ አሶርን ያጠቃሉ ዔቦርን ይይዛሉ፣ ነገር ግን እነርሱም ደግሞ መጨረሻቸው መደምሰስ ነው፡፡ 25 ከዚያ በለዓም ተነስቶ ሄደ፡፡ ወደ ቤቱ ተመለሰ፣ ባላቅም ተነስቶ ሄደ፡፡



Numbers 24:2

ዓይኖቹን አነሳ

“ዓይኖቹን አነሳ”የሚለው ቃል ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ወደ ላይ መመልከት ማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔርም መንፈስ በእርሱ ላይ መጣ

ይሄ ማለት ትንቢትን መናገር ይችል ዘንድ የእግዚአብሔር መንፈስ ሙሉ በሙሉ ተቆጣጠረው ማለት ነው፡፡

ይህንን ትንቢት ተቀበለ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ይህንን ትንቢት ሰጠው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የቢዖር ልጅ በለዓም

ቢዖር የበለዓም አባት ነበር፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ዓይኖቹ የተከፈቱለት

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያሣየው በሚገባ ማየቱንና መገንዘቡን ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:4

አጠቃላይ መረጃ

በለዓም በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር ሆኖ ትንቢት መናገሩን ይቀጥላል፡፡

እርሱ ይናገራል…እርሱ ያያል…እርሱ ይሰግዳል

እዚህ ላይ በለዓም ራሱን የሚጠራው“እርሱ” እያለ ነው፡፡

እርሱ ይሰግዳል

ይሄ የትህትና ድርጊት ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

ዓይኖቹ የተከፈቱለት

“ዓይኖቹ የተከፈቱለት”የሚለው ቃል ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን በለዓም እግዚአብሔር መናገር የፈለገውን ነገር የማወቅ ችሎታ ተሰጥቶታል ለማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ያዕቆብ ሆይ ድንኳኖችህ፤እሥራኤል ሆይ ማደሪያዎችህ ምንኛ ያምራሉ?

እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡ለበለዓም የእሥራኤል ሰፈር ውብ እንደሆነበት አስረግጠው የሚናገሩ ናቸው፡፡ (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:6

አጠቃላይ መረጃ

በለዓም በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር ሆኖ ትንቢት መናገሩን ይቀጥላል፡፡

በሸለቆዎች ተዘርግተዋል

በለዓም እሥራኤልን በሚመለከት ሸለቆዎቸን እንኳን መሸፈን እስኪችሉ ድረስ ዘንድ በቁጥር እጅግ ብዙ እንደሆኑ አድርጎ ነው የሚናገረው፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

በወንዝ ዳር እንዳሉ አትክልቶች

በለዓም እሥራኤላውያንን በቂ ውኃ እንደሚጠጡና የተትረፈረፈ ምርትን እንደሚያስገኙ አትክልቶች አድርጎ ያቀርባቸዋል፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር እንደተከለው እሬት

የእሬት አትከልቶች መልካም የሆነ ሽታ ያላቸው በደረቅ የአየር ሁኔታ ውስጥ እንኳን በሚገባ ማደግ የሚችሉ ናቸው፡፡በለዓም እሥራኤላውያን እንደ እሬት አትክልቶች እንደሚያድጉና መልካም እንደሚሆኑይናገራል፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር የተከለው እሬት”(ያልታወቁ ነገሮችን መተርጎም፤ተነፃፃሪ የሚለውንና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በውኃም ዳር እንዳሉ ዘግባዎች

ዝግባ በእሥራኤል ውስጥ ከነበሩት ዛፎች ትልቁ ነው፡፡በለዓም እሥራኤላውያን ልክ ውኃ እንደሚጠጣ ዝግባ ዛፍ ግዙፍ ሆነው እንዳደጉ ዓይነት አድርጎ ይናገራል፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:7

አጠቃላይ መረጃ

በለዓም በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር ሆኖ ትንቢት መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ውኃ ይፈስሳል…በብዙ ውኆች ይሆናል

ብዛት ያለው ውኃ በምድር ላይ እንዳሉና እግዚአብሔር እንደባረካቸው ሰብሎች ተቆጥሯል፡፡“እግዚአብሔር ለሰበሎቻቸው ይሆን ዘንድ ብዙ ውኃ በመሥጠት ይባርካቸዋል”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ዘሩም በብዙ ውሆች ይሆናል

በሚገባ ውኃ የጠጣ ዘር የሚለው ቃል የሚያመለክተው የተትረፈረፈ ሰብል ይኖራቸው ዘንድ የእግዚአብሔር በረከት በእነርሱ ላይ የሚመጣ መሆኑን ነው፡፡“ጤናማ የሆኑ ሰብሎችን ያበቅሉ ዘንድ ለሚዘሩት ዘር ከበቂ በላይ የሆነ ውኃን ያገኛሉ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ንጉሡም ከፍ ከፍ ይላል…መንግሥቱም ይከበራል

እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ከሌሎች አገራት ይልቅ እጅግ እንደሚባርካቸው አፅንዖት የሚሰጥ ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ንጉሥም ከአጋግ ይልቅ ከፍ ከፍ ይላል

“ከፍ ከፍ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ታላቅ የሆነ ክብርና ሥልጣንን ነው፡፡ይሄ የሚያመለክተው ወደፊት የሚነሣው የእሥራኤል ንጉሥ ከአጋግ ይልቅ የበለጠ ክብርና ሥልጣን የሚኖረው መሆኑን ነው፡፡አጋግ የአማሌቃውያን ንጉሥ ነበር፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና (ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ))

መንግሥቱም ይከበራል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሌሎች ሰዎች ለመንግሥታቸው ክብርን ይሰጣሉ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:8

አጠቃላይ መረጃ

በለዓም በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር ሆኖ ትንቢት መናገሩን ይቀጥላል፡፡

እግዚአብሔር አውጥቶታል

“እግዚአብሔር እሥራኤላውያንን አውጥቷቸዋል”

ጉልበቱ አንድ ቀንድ እንዳለው ነው

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር አፅንዖት የሚሰጠው እሥራኤላውያን ታላቅ የሆነ ጉልበት ያላቸው መሆኑን ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ጠላቶቹን አህዛብን ይበላል

በለዓም እሥራኤላውያንን ልክ ዱር አውሬዎች ጠላቶቻቸውን ከሚበሉት አበላል ጋር አነፃፅሯቸዋል፡፡ይሄ ማለት ጠላቶቻቸውን ያጠፏቸዋል ማለት ነው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:9

አጠቃላይ መረጃ

በለዓም በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር ሆኖ ትንቢት መናገሩን ይቀጥላል፡፡

እንደ አንበሳ አርፎ ተኝቷል፤እንደ እንስቲቱም አንበሳ ተጋድሟል

በዚህ ፈሊጣዊ አነጋገር ውስጥ በለዓም እሥራኤላውያንን ከሴትና ከወንድ አንበሳ ጋር መሳስላቸዋል፡፡ይሄ ማለት አደገኞችና ሁልጊዜ ለማጥቃት ዝግጁ ናቸው ማለት ነው፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

ማን ያስነሣዋል?

በለዓም ይህንን ጥያቄ የሚያነሳው ማንም ሰው ቢሆን እሥራኤልን እንዳያስቆጣ ለማስጠንቀቅ ነው፡፡ይሄ በዐረፍተ ነገር መልክ ሊተረጎም ይችላል፡፡“ማንም ቢሆን እርሱን ለመረበሽ ድፍረቱ አይኖረውም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

የሚመርቅህ ሁሉ የተመረቀ ይሁን፤የሚረግምህም ሁሉ የተረገመ ይሁን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር እሥራኤላውያንን የሚባርኩትን ይባርክ፤የሚረግሙትንም ይርገም”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:10

የባላቅ ቁጣ ነደደ

የባላቅ ቁጣ የመንደዱ ጉዳይ ልክ ሊነድድ እነደጀመረ ዓይነት እሣትተደርጎ ተገልጿል፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ባላቅ በኃይል ተናደደ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እጆቹንም አጨበጨበ

ይሄ የታላቅ ብስጭትና ንዴት ምልክት ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:12

ባላቅ በቤቱ የሞላውን ብርና ወርቅ ቢሰጠኝ

ባላቅ እየገለፀ ያለው ፈፅሞ ሊሆን የማይችልን ነገር ነው፡፡ይሄ ዓረፍተ ነገር አስረግጦ የሚናገረው በምንም ዓይነት መንገድ በለዓም ለእግዚአብሔር እንዳይታዝ የሚያደርገው ነገር የማይኖር መሆኑን ነው፡፡(ምናባዊ ሁኔታዎች)

ለላክሃቸው አልተናገርኩምን?

በለዓም ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው ቀደም ሲል የተናገረውን ለባላቅ ለማሳሰብ ነው፡፡ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ በዓረፍተ ነገር መልክም ሊተረጎም ይችላል፡፡“ይህንን ነግሬያቸዋለሁ”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ይሄ ሕዝብ

“እሥራኤላውያን”

Numbers 24:15

የቢዖር ልጅ በለዓም

ቢዖር በለዓም አባት ነበረ፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ዓይኖቹም የተከፈቱለት

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው በሚገባ የሚያይና የሚረዳ መሆኑን ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 24፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የልዑልንም ዕውቀት የሚያውቅ

“ዕውቀት”የሚለው ረቂቅ ሥም በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ታላቁ እግዚአብሔር የገለጠለትን ነገር የሚያውቅ ሰው”(አሕፅሮተ ሥሞች የሚለውን ይመልከቱ)

ይሰግዳል

ይሄ ለእግዚአብሔር የመገዛት ምልክት ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:17

አጠቃላይ መረጃ

በለዓም ከአራቱ ትንቢቶች መካከል አንዱን መናገር ይጀምራል፡፡

እርሱን አየዋለሁ አሁን ግን አይደለም፤እርሱን እመለከተዋለሁ በቅርብ ግን አይደለም

እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡በለዓም ወደፊት ስለሚከሰተው ነገር ራዕይ አየተመለከተ ነው፡፡“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የወደፊቱን የእሥራኤል መሪ ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል

እዚህ ላይ“ኮከብ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በእሥራኤል ላይ ሥልጣን የሚይዘውን ንጉሥ ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ቋንቋ የሚለውን ይመልከቱ)

ከያዕቆብ

እዚህ ላይ“ያዕቆብ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የያዕቆብን ትውልድ ነው፡፡“ከያዕቆብ ትውልድ መካከል”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ከእሥራኤል በትር ይነሳል

ይሄ ከመጀመሪው ዓረፍተ ነገር ጋር ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያለው፡፡እዚህ ላይ “በትር”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ብርቱ የሆነ ንጉሥን ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ከእሥራኤል

እዚህ ላይ“እሥራኤል”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የወደፊት እሥራኤላውያንን ነው፡፡“ወደፊት ከሚወለዱት እሥራኤላውያን መካከል”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የሞዓብንም ማዕዘኖች ይመታል

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/ሞዓብ መሪዎችን አናት ይመታል2/የሞዓብን መሪዎች ያጠፋል፡፡

የሤትንም ልጆች

ይሄ የሤት ዝርያዎች የሆኑ ሞአባውያንን የሚመለከት ነው፡፡

Numbers 24:18

አጠቃላይ መረጃ

በለዓም የመጀመሪዎቹን አራት ትንቢቶች መናገር ያበቃል፡፡

ኤዶም ርስቱ ይሆናል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እሥራኤላውያን ኤዶምን በቁጥጥራቸው ሥር ያደርጓታል፡፡”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:20

በለዓም አማሌቅን አይቶ

እዚህ ላይ“አማሌቅ የሚለው ቃል የሚያመለክተው የአማሌቅን ሕዝብ ነው፡፡ራዕዩ የቀጠለው ወደ አሜሌቃውያን አቅጣጫ ከተመለከተ በኋላ ሲሆን ከዚያ በኋላ ስለ አማሌቃውያን መተንበዩን ይቀጥላል”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የእርሱ ፍፃሜ ግን

ነጠላ ሥም ጥቅም ላይ የዋለበት ምክኒያት አማሌቃውያን እንደ አንድ ግለሰብ በመታየታቸው ነው፡፡(የመጀመሪያ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ አካል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:21

ቄናውያን

ይሄ ሥም የቃየን ትውልድ ሆነ ሕዝብ ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ማደሪያህ የፀና ነው

“የምትኖርበት ሥፍራ ከባድ መከላከያ ያለው ነው”

ጎጆህም በአምባ ላይ ተሰርቷል

ይሄ ምሣሌያዊ አነጋገር ሲሆን ደህንነቱ በተጠበቀ ሥፍራ ላይ መኖር ማለት ነው፡፡“የምትኖርበት ሥፍራ ዓለታማ በሆኑ ከፍታ ሥፍራዎች ላይ እንዳለ ወፍ ጎጆ ደህንነቱ የተጠበቀ ነው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ነገር ግን አሦር እስኪማርክህ ድረስ ቄናዊው ለጥፋት ይሆናል

እዚሀ ላይ የቄናውያን መጥፋት በእሣት እንደሚቃጠሉ ዓይነት ሆኖ ተገልጿል፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ነገር ግን እናንተ ቄናዊያን አሦራውያን አንድ ነገር በእሣት እንደሚጠፋ ያጠፏችኋል፤በምርኮኝነትም ይወስዷኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 24:23

እገዚአብሔር ይህንን ሲያደርግ አወይ ማን በይወት ይኖራል?

ይሄ አስፈላጊ የሆነ ጥያቄ በዓረፍተ ነገር መልክ ሊተረጎም ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ይህንን በሚያደርግበት ወቅት ማንም በሕይወት አይኖርም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ኪቲም

ይሄ በሜዲተራንያን ባህር ውስጥ የሚገኝ የአንድ ደሴት ከተማ ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱም ደግሞ ወደ ጥፋት ይመጣሉ

“ጥፋት”የሚለው ረቂቅ ሥም በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር እነርሱንም ያጠፋቸዋል”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ባላቅ

ይሄ የሞአብ ንጉሥ ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡


Chapter 25

1 እስራኤል በሰጢም ተቀመጠ፣ ወንዶቹም ከሞዓብ ሴቶች ጋር ተኙ፣ 2 ይህም ሞአባዊያኑ ህዝቡን ለእነርሱ አማልዕክት የተሰዋውን ስለጋበዟቸው ነው፡፡ ስለዚህ ህዝቡ ለጣኦት የተሰዋውን በሉ ደግሞም ለሞአባውያን አማልዕክት ሰገዱ፡፡ 3 የእስራኤል ወንዶች የፌጎርን በኣል በማምለክ ተባበሩ፣ እናም የያህዌ ቁጣ በእስራኤል ላይ ነደደ፡፡ 4 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “ብርቱ ቁጣዬ ከእስራኤል ይርቅ ዘንድ የህዝቡን መሪዎች ሁሉ ግደልና እነርሱን በቀን ብርሃን ለማጋለጥ ስቀላቸው፡፡” 5 ስለዚህም ሙሴ ለእስራኤል መሪዎች እንዲህ አለ፣ “እያንዳንዳችሁ የፌጎርን በኣል በማመልክ የተባበሩትን ሰዎቻችሁን ግደሉ፡፡” 6 ከዚያ ከእስራኤል ወንዶች አንዱ ቀርቦ ከቤተሰቡ አባላት ጋር አንዲት ምድያማዊት ሴት አመጣ፡፡ ሙሴና መላው የእስራኤል ህዝብ እያዩ በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ሆነው እያለቀሱ ሳለ ይህ ሆነ፡፡ 7 የአሮን ልጅ፣ የአልዓዛር ልጅ ካህኑ ፊንሀስ ይህን ሲመለከት፣ ከማህበሩ መሀል ጦሩን በእጁ ይዞ ተነሳ፡፡ 8 እርሱም ወደ ድንኳኑ እስራኤላዊውን ሰው ተከትሎ ገብቶ የእስራኤላዊውን ወንድና የምድያማዊቷን ሴት የሁለቱንም አካላት በአንድነት በጦሩ ወጋ፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር በእስራኤል ህዝብ ላይ የላከው መቅሰፍት አቆመ፡፡ 9 በመቅሰፍቱ የሞቱት በቁጥር ሃያ አራት ሺ ነበሩ፡፡ 10 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 11 “ካህኑ፣ የአሮን ልጅ የአልአዛር ልጅ ፊንሀስ፣ ቁጣዬን ከእስራኤል ህዝብ አርቋል ምክንያቱም በእነርሱ መሃል የእኔን ቅንአት ቀንቷል፡፡ ስለዚህ የእስራኤልን ህዝብ በቁጣዬ ፈጽሞ አላጠፋኋቸውም፡፡ 12 ስለዚህ እንዲህ በል፣ ‘ያህዌ እንዲህ ይላል፣ “እነሆ፣ ለፊንሐስ የሰላሜን ኪዳን እሰጠዋለሁ፡፡ 13 ለእርሱና ከእርሱ በኋላ ለትውልዱ፣ ዘለዓለማዊ የክህነት ኪዳን ይሆናል፤ ምክንያቱም እርሱ ለእኔ ለአምላኩ ለእግዚአብሔር ቀንቷል፡፡ ለእስራኤል ህዝብ አስተሰርይዋል፡፡” 14 ከምድያማዊቷ ሴት ጋር የተገደለው የእስራኤላዊ ሰው የሰሉ ልጅ ስም ዘንበሪ ሲባል፣ የስምኦናውያን አባቶች ቤተሰብ መሪ ነበር፡፡ 15 የተገደለችው የምድያም ሴት ስም ከስቢ ነበር፣ እርሷም ከምድያም ቤተሰብ የጎሳው መሪ የሱር ሴት ልጅ ነበረች፡፡ 16 ስለዚህም ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 17 ”ምድያማዊያንን እንደ ጠላት ቆጥራችሁ አጥፏቸው፣ 18 እነርሱ በአታላይነታቸው እንደ ጠላት አስተናግደዋችኋልና፡፡ በፌጎር በሆነውና በእናታቸው በከስቢ ጉዳይ በፌጎር ምክንያት በመቅሰፍቱ ቀን በተገደለችው በምድያም አለቃ ልጅ ወደ ክፉ መርተዋችኋል፡፡”



Numbers 25:1

ሰጢም

ይሄ በሞአብ ውስጥ የሚገኝ የቦታ ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰገዱ

ይሄ የአምልኮ ሥርዓት ድርጊት ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

ብኤልፌጎር

ብኤልፌጎር የተራራ ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 23፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የእግዚአብሔርም ቁጣ ነደደ

የእግዚአብሔር ቁጣ መንደድ ከሚጀምር እሣት ጋር ተመሳስሎ ተነግሯል፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ይህንንሐረግ በዘኁልቁ 22፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“እግዚአብሔር በጣም ተናደደ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውንና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 25:4

የእሥራኤል መሪዎች ሁሉ

ይሄ የሚያመለክተው ጣዖትን በማምለክ ጥፋተኛ የሆኑ መሪዎችን ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ጣዖትን በማምለክ ጥፋተኛ የሆኑ የሕዝብ መሪዎች ሁሉ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በፀሐዩ ፊት ወስደህ

ይሄ ማለት የሕዝቡ መሪዎች እነዚህን ሰዎች ከገደሉ በኋላ ሬሣቸውን ሰዎች ሁሉ ሊያዩ በሚችሉበት ሥፍራ ላይ ይተውታል ማለት ነው፡፡

የእሥራኤል መሪዎች

“በጣዖት አምልኮ ውስጥ ያልተሳተፉ የእሥራኤል መሪዎች”

ፌጎር

ፌጎር የተራራ ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 23፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 25:6

ምድያማዊቱን አንዲቱን ሴት ወደ ወንድሞቹ አመጣት

ይሄ የሚያመለክተው ወደ ሠፈሩ ከአርሷ ጋር ወሲባዊ ግንኙነት ለማድረግ ወደ ሠፈሩ ይዟት መምጣቱን ነው፡፡የዚህ ሙሉ ትርጉም የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ከምድያማዊቷ ሴት ጋር አብሮ ለመተኛት ወደ እሥራኤላውያን ሠፈር አመጣት”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሥራኤል ልጆች ማህበር ዓይን ፊት

“ዓይን ፊት” የሚለው ቃል ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ስለ ጉዳዩ ሰምተዋል ወይም ጉዳዩን አውቃውታል ማለት ነው፡፡

አልዓዛር

ይሄ የአሮን ልጅ ሥም ነው፡፡ይህንን በዘኁልቁ 3፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 25:8

ተከትሎ ገባ

“ፊንሐስ ተከትሎ ገባ”

Numbers 25:10

ቁጣዬን ከእሥራኤል ልጆች መለሰ

የእግዚአበሔር ቁጣ ለመቆም እንዲችል ወደ አንድ ሥፍራ በአካል መገፋት እንዳለበት ዓይነት ነገር ተደርጎ ነው የሚነገረው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እኔም የእሥራኤልን ልጆች በቅንዓቴ አላጠፋሁም

እግዚአብሔር እዚሀ ላይ የተገለፀው ልክ የእሥራኤልን ሕዝብ እንደሚበላ ጨካኝ አውሬ ተደርጎ ነው፡፡“በእጅጉ የተናደድኩ ቢሆንም የእሥራኤልን ሕዝብ ግን አላጠፋሁም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 25:12

ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡፡ለፊንሐስ እሰጠዋለሁ…የእሥራኤልን ሕዝብ

ይሄ የእግዚአብሔርን ንግገር ካለፈው ጥቅስ እንዲቀጥል ያደርገዋል፡፡ይሄ በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ አለው፡፡ቀጥተኛ የሆኑት ጥቅሶች ቀጥተኛ እንዳልሆኑ ጥቅሶች ሊገለፁ ይችላሉ፡፡(በጥቅሶች ውስጥ ጥቅሶችና ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆኑ ጥቅሶች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 25:14

አሁን

ይሄ ዋናውን ታሪክ ወደ ጀርባ ታሪክ በመቀየር ስለ ዘንበሪና ስለ ከስቢ ያወሳል፡፡(የጀርባ ታሪክ የሚለውን ይመልከቱ)

የተገደለው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ፊንሐስ የገደለው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ዘንበሪ…ሰሉ…ሱር

እነዚህ የሰው ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ከስቢ

ይሄ የአንዲት ሴት ሥም ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 25:16

በሸነገሉት ሽንገላ

“መሽንገል”የሚለው ረቂቅ ሥም እንደ ሥም ሊገለፅ ይችላል፡፡“እናንተን በማታለል”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ ክፋት መሯችሁ

“ይህንን ክፉ ሥራ እንድትሰሩ አግቧቧችሁ”

በፌጎር ጉዳይ ..በፌጎር ነገር

እነዚህ ሁለቱም ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ሃሣብ ያላቸው ሲሆን እነዚህ ነገሮች የተከናወኑት በፌጎር ተራራ እንደሆነ ይገልፃሉ፡፡

ፌጎር

ፌጎር የተራራ ሥም ነበር፡፡ይህንን በዘኁልቁ 23፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የተገደለው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ፊንሐስ የገደለው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 26

1 ከመቅሰፍቱ በኋላ እንዲህ ሆነ፣ ያህዌ ለሙሴና ለካህኑ ለአሮን ልጅ ለአልዓዛር እንዲህ አላቸው፡፡ 2 “የእስራኤልን ማህበረሰብ ሁሉ ቁጠሩ፣ ሀያ አመትና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላቸውን፣ ለእስራኤል ለመዋጋት ወደ ጦርነት መውጣት የሚችሉትን ሁሉ በየአባቶቻቸው ቤቶች ቁጠሯቸው፡፡” 3 ስለዚህም ሙሴና ካህኑ አልዓዛር በሞአብ ሜዳ በዮርዳኖስ አጠገብ ኢያሪኮ ሳለ ለህዝቡ እንዲህ ሲሉ ተናገሩ፣ 4 “ከሃያ አመት ጀምሮ ከዚያ በላይ ዕድሜ ያላቸውን ከግብጽ ምድር የወጡትን ያህዌ ሙሴንና የእስራኤል ሰዎችን እንዳዘዘው ሁሉ ቁጠሯቸው፡፡” 5 ሮቤል የእስራኤል በኩር ነበር፡፡ ከወንድ ልጁ ከሄኖክ የሄኖካውያን ጎሳዎች መጡ፡፡ ከፈለስ የፈለሳውያን ጎሳ መጡ፡፡ 6 ከአስሮን የአስሮናውያን ጎሳ መጡ፡፡ ከከርሚ የከርማውያን ጎሳ መጡ፡፡ 7 እነዚህ የሮቤል ጎሳ ትውልዶች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 43730 ወንዶች ነበሩ፡፡ 8 ኤልያብ የፈሉስ ልጅ ነበር፡፡ 9 የኤልያብ ወንዶች ልጆች ነሙኤል፣ ዳታን፣ እና አቤሮን ነበሩ፡፡ እነዚህ ቆሬን ተከትለው ሙሴንና አሮንን በመቃወም በያህዌ ላይ ያመጹት እነዚያው ዳታንና ኤብሮን ነበሩ፡፡ 10 ሁሉም የእርሱ ተከታዮች ሲሞቱ፣ ምድር አፏን ከፍታ ከቆሬ ጋር ሁሉንም በአንድነት ዋጠቻቸው፡፡ በዚያ ጊዜ፣ በእሳት መቀጣጫ የሆኑትን 250 ወንዶችን በላች፡፡ 11 ነገር ግን የቆሬ የዘር ሀረግ አልጠፋም፡፡ 12 የስምዖን ትውልዶች እዚህ ነበሩ፡ በነሙኤል በኩል፣ የነሙኤላውያን ጎሳ፣ በያሚን በኩል፣ የያሚናውያን ጎሳ፣ በያኪን በኩል የያኪናውያን ጎሳ፣ 13 በዛራ በኩል የዛራውያን ጎሳ፣ በሳኡል በኩል የሳኡላውያን ጎሳ ነበሩ፡፡ 14 እነዚህ የስምዖን ጎሳ ትውልዶች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 22200 ወንዶች ነበሩ፡፡ 15 የጋድ ጎሳ ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በጽፎን በኩል የጽፎናውያን ጎሳ፣ በሐጊ በኩል የሐጋውያን ጎሳ፣ በሺኒ በኩል፣ የሺናውያን ጎሳ፣ 16 በኤስና በኩል፣ የኤሶናውያን ጎሳ፣ በዔሪ በኩል የዔራውያን ጎሣ፣ 17 በአሮዲ በኩል የሮዳውያን ጎሳ፣ በአርኤሊ በኩል፣ የአርኤላውያን ጎሳ፡፡ 18 እነዚህ የጋድ ጎሳ ትውልድ ነበሩ፣ ቁጥራቸው 40500 ወንዶች ነበሩ፡፡ 19 የይሁዳ ልጆች ዔር እና አውናን ነበሩ፣ እነዚህ ወንዶች ግን በከነዓን ምድር ሞተዋል፡፡ 20 የይሁዳ ጎሳ ሌሎች ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፣ በሴሎም በኩል፣ የሴሎማውያን ጎሳ፣ በፋሬስ በኩል፣ የፋሬሳውያን ጎሳ፣ እና በዛራ በኩል የዛራውያን ጎሳ ነበሩ፡፡ 21 የፋሬስ ትውልዶች እነዚህ ነበሩ በኤስሮም በኩል የኤስሮማውያን ጎሳ፣ በሐሙል በኩል፣ የሐሙላውያን ጎሳ፡፡ 22 እነዚህ የይሁዳ ጎሳ ትውልዶች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 76500 ነበሩ፡፡ 23 የይሳኮር ጎሳዎች ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡፡ በቶላ በኩል የቶላውያን ጎሳ፣ በፋዋ በኩል ቦፋውያን ጎሳ፣ 24 በያሱብ በኩል፣ የያሱባውዩን ጎሳ፣ በሺምሮን በኩል፣ የሺምሮናውያን ጎሳ፡፡ 25 እነዚህ የይሳኮር ጎሳዎች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 64300 ወንዶች ነበሩ፡፡ 26 የዛብሎን ጎሳዎች ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡፡ በሴሬድ በኩል የሴሬዳውያን ጎሳ፣ በኤሎን በኩል የኤሎናውያን ጎሳ፣ በያህልኤል በኩል የያህልኤላውያን ጎሳ፡፡ 27 እነዚህ የዛብሎን ጎሳዎች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 60500 ወንዶች ነበሩ፡፡ 28 የዮሴፍ ጎሳ ትውልዶች ምናሴና ኤፍሬም ነበሩ፡፡ 29 የምናሴ ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በማኪር በኩል፣ የማኪራውያን ጎሳ (ማኪር የገለዓድ አባት ነበር) ፣ በገለዓድ በኩል፣ የገለዓዳውያን ጎሳ ነበሩ፡፡ 30 ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በኢዔዝር በኩል የኢዔዝራውያን ጎሳ፣ በኬሌግ በኩል የኬሌጋውያን ጎሳ፣ 31 በእስራኤል በኩል የእስራኤላውያን ጎሳ፣ በሴኬም በኩል፣ የሴካማውያን ጎሳ፣ 32 በሸሚዳ በኩል፣ የሸሚዳውያን ጎሣ፣ በኦፌር በኩል የኦፌራውያን ጎሣ፣ 33 ልጅ ሰለጳዓድ ወንዶች ልጆች አልነበሩትም፣ ነገር ግን ሴቶች ልጆች ብቻ ነበሩት፡፡ የሴት ልጆቹ ስሞች እነዚህ ነበሩ፡ ማህለህ፣ ኑዓ፣ ዔግሳ፣ ሚልካና ቲርዳ፡፡ 34 እነዚህ የምናሴ ጎሳዎች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 52700 ወንዶች ነበሩ፡፡ 35 የኤፍሬም ጎሳዎች ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በሲቱላ በኩል፣ የሱቱላውያን ጎሣ፣ በቤኬር በኩል የቤኬራውያን ጎሣ፣ በታሐን በኩል፣ የታሐናውያን ጎሣ ነበሩ፡፡ 36 የሱቱላ ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በዔዴን በኩል፣ የዔዴናውያን ጎሣ ነበሩ፡፡ 37 እነዚህ የኤፍሬም ጎሣ ትውልዶች ነበሩ፡ ቁጥራቸው 32500 ወንዶች ነበሩ፡፡ እነዚህ የዮሴፍ ትውልዶች፣ በየጎሣቸው ተቆጠሩ፡፡ 38 የብንያም ጎሣ ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በቤላ በኩል፣ የቤላውያን ጎሣ፣ በአስቤል በኩል የአስቤላውያን ጎሣ፣ በኢኪራን በኩል፣ የኢኪራናውያን ጎሣ፣ 39 በሶፋን በኩል፣ የሶፋናውያን ጎሣ፣ በሑፋም በኩል፣ የሑፋፋማውያን ጎሣ ነበሩ፡፡ 40 የቤላ ወንዶች ልጆች አርድ እና ናዕመን ነበሩ፡፡ ከአርድ የአርዳውያን ጎሣ መጣ፣ ከናዕማን የናዕመናውያን ጎሣ መጣ፡፡ 41 የብንያም ጎሣ ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡፡ ቁጥቸው 45600 ወንዶች ነበሩ፡፡ 42 የዳን ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በስምዔ በኩል፣ የስምዔያናውያን ጎሣዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ የዳን ትውልድ ጎሣዎች ነበሩ፡፡ 43 የስምዔያውያን ጎሣዎች በጠቅላላ 64400 ወንዶች ነበሩ፡፡ 44 የአሴር ትውልድ ጎሣዎች እነዚህ ነበሩ፡ በዩምና በኩል የዩምናውያን ጎሣ፣ በዩሱዋ በኩል፣ የየሱዋውያን ጎሣ፣ በበሪዓ በኩል፣ የበሪዓውያን ጎሣ ነበሩ፡፡ 45 የብንያም ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በሔቤር በኩል፣ የሔቤራውያን ጎሣ፣ በመልኪኤል በኩል የመልኪኤላውያን ጎሣ ነበሩ፡፡ 46 የአሴር ሴት ልጅ ስም ሤራህ ነበር፡፡ 47 እነዚህ የአሴር ጎሣ ትውልዶች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 53400 ወንዶች ነበር፡፡ 48 የንፍታም ጎሣ ትውልዶች እነዚህ ነበሩ፡ በያሕድኤል በኩል፣ የያህጽኤላውያን ጎሣ፣ በጉኒ በኩል፣ የጉናውያን ጎሣ፣ 49 በሺሌም በኩል፣ የሺሌማውያን ጎሣ ነበሩ፡፡ 50 እነዚህ የንፍታሌም ጎሣ ትውልዶች ነበሩ፣ ቁጥራቸው 45400 ወንዶች ነበር፡፡ 51 ይህ በእስራኤል ህዝብ መሃል ጠቅላላው የወንዶች ቁጥር ነበር፡፡በጠቅላላው 601730 ነበሩ፡፡ 52 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፣ 53 “ምድሪቱ በእነዚህ ሰዎች መሃል ርስት ሆኖ እንደ ስሞቻቸው ቁጥር መሰረት ትከፋፈል፡፡ 54 ብዙ ቁጥር ላለው ጎሳ ሰፋ ያለውን ርስት ስጥ፣ አነስተኛ ቁጥር ላላቸው ጎሣዎች አነስ ያለውን ርስት ስጣቸው ለእያንዳንዱ ቤተሰብ እንደ ተቆጠረው ወንድ ብዛት ርስት ስጣቸው፡፡ 55 ሆኖም ምድሪቱ በዕጣ ትከፋፈል፡፡ ምድሪቱን በየአባቶቸው ጎሳዎች መሀል እንደምትከፋፈል ይወርሷት፡፡ 56 ርስታቸው በየጎሳው ብዛትና አነስተኛት መጠን ይከፋፈል፣ ክፍፍሉ በዕጣ ይሁን፡፡” 57 በየነገዳቸው የተቆጠሩት የሌዋውያን ነገዶች እነዚህ ነበሩ፡ በጌድሶን በኩል፣ የጌድሶናውያን ጎሣ፣ በቀዓት በኩል፣ የቀዓታውያን ጎሣ፣ በሜራሪ በኩል፣ የሜራርያውን ጎሣ ነበሩ፡፡ 58 የሌዊ ጎሳዎች እነዚህ ነበሩ፡ የሊብናውያን ጎሣ፣ የኬብሮናውያን ጎሣ፣ የሞሐላውያን ጎሣ፣ የሙሳውያን ጎሣ፣ እና የቆሬያውያን ጎሣ ነበሩ፡፡ ቀዓት የእንበረም የዘር ሀረግ ነበር፡፡ 59 የእንበረም ሚስት ስሟ ዮካብድ ነበር፣ ከሌዋውያን ወገን ግብጽ ውስጥ የተወለደች ነበረች፡፡ ከእንበረም ልጆቻቸውን አሮንን፣ ሙሴን እና እህታቸውን ማርያምን ወለደች፡፡ 60 ለአሮን የተወለዱለት ናዳብ እና አብዩድ፣ ኤልዓዛር እና ኢታምር ነበሩ፡፡ 61 ናዳብና አብዩድ ያህዌ በፊቱ ተቀባይነት የሌለውን የእሳት መስዋዕት ሲያቀርቡ ሞቱ፡፡ 62 አንድ ወርና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያቸው ሌዋውያን ወንዶች ቁጥር ሃያ ሶስት ሺ ነበር፡፡ ነገር ግን ከእስራኤል ትውልዶች ጋር አብረው አልተቆጠሩም፡፡ ምክንያቱም ለእነርሱ በእስራኤል ሕዝብ መሃል ምንም ርስት አልተሰጣቸውም ነበር፡፡ 63 በሙሴና በካህኑ አልዓዛር የተቆጠሩት እነዚህ ናቸው፡፡ በሞአብ ሜዳ በዮርዳኖስ ኢያሪኮ ውስጥ የእስራኤልን ህዝበ ቆጠሩ፡፡ 64 የእስራአል ትውልዶች በሲና ምድረ በዳ በተቆጠሩ ጊዜ በእነዚህ መሀል በሙሴና በካህኑ በአልዓዛር የተቆጠረ ሌላ ሰው ግን አልነበረም፡፡ 65 ያህዌ እነዚያ ሰዎች ሁሉ በእርግጥ በምድረበዳ እንደሚሞቱ ተናግሮ ነበር፡፡ ከዩፎኒ ልጅ ከካሌብና ከነዌ ልጅ ከኢያሱ በስተቀር ከመሀላቸው በህይወት የተረፈ አንድም ሰው አልነበረም፡፡



Numbers 26:1

ማህበሩን ሁሉ ቁጠር

የሚቆጥሩት ሴቶችን ሣይሆን ወንዶችን ብቻ ነበር፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ትርጉም የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“በማህበሩ ውሰጥ ያሉትን ወንዶች ሁሉ ቁጠሩ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሃያ ዓመት ጀምሮ ከዚያ በላይ

“20 ዓመትና ከዚያ በላይ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:3

“ተናገሯቸው”

ለእሥራኤል መሪዎች ተናገሩ፡፡

ሜዳ

ሜዳ ሠፊና ለጥ ያለ መሬት ነው፡፡

ሃያ ዓመትና ከዚያም በላይ

“20 ዓመትና ከዚያም በላይ”

Numbers 26:5

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል በኩር ነበረ

እዚህ ላይ እሥራኤል የሚለው ቃል የሚያመለክተው ያዕቆብ በመባል የሚታወቀውን ሰው ነው፡፡

ከእርሱ ወንድ ልጁ

እዚህ ላይ“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሮቤልን ነው፡፡

43,730

“አርባ ሶስት ሺህ ሰባት መቶ ሰላሣ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:8

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ኤልያብ… ዳታን… አቢሮን

የእነዚህን ሰዎች ሥም በዘኁልቁ 16፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 26:10

ምድሪቱ አፍዋን ከፍታ ዋጠቻቸው

እዚህ ላይ ምድሪቱ የተቆጠረችው ልክ አንድ ሰው አፉን ከፍቶ አንድን ነገር እንደሚበላ ዓይነት ነው፡፡“እግዚአብሔር ምድሪቱ እንድትከፈት ካደረገ በኋላ ሰዎቹ በዚያ ጉድጓድ ውስጥ ወደቁ”(ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

እሣቲቱም 250 ሰዎችን በላቻቸው

እዚህ ላይ እሣቱ የተገለፀው ልክ አንድ ትልቅ እንስሳ አንድን ነገር እንደሚውጥ ተደርጎ ነው፡፡ “እግዚአብሔር 250 ሰዎችን ለመግደል እሣትን ተጠቀመ”(ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

250 ሰዎች

“ሁለት መቶ ሃምሣ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የቆሬ ወገኖች

“የቆሬ ቤተሰቦች በሙሉ”

ዋጠቻቸው

“መጨረሻቸው ሆነ”

Numbers 26:12

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

22,200 ሰዎች

“ሃያ ሁለት ሰሺህ ሁለት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:15

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

40,500 ሰዎች

“አርባ ሺህ አምስተ መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:19

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

76,500 ሰዎች

“ሰባ ስድስት ሺህ አምስት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:23

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

64,300 ሰዎች

“ስድሳ አራት ሺህ ሶስት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:26

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

60,500 ሰዎች

“ስድሳ ሺህ አምስት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:28

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንይመልከቱ)

Numbers 26:30

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:33

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

52,700 ሰዎች

“አምሳ ሁለት ሺህ ሰባት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:35

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

32,500 ሰዎች

“ሰላሳ ሁለት ሺህ አምስት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

እነዚህ የተቆጠሩት የዮሴፍ ወገኖች ናቸው

“እነዚህ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የዮሴፍ ልጆች ከሆኑት ከኤፈሬምና ከምናሴ ልጆች የተወለዱትን ትውልድ ሁሉ ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊበራራ ይችላል፡፡“እነዚህ የያዕቆብ ልጆች ከሆኑት ከኤፍሬምና ከምናሴ ዘር የተገኙ ናቸው፡፡እነርሱም ተቆጠሩ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በየወገናቸው ተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በየወገናቸው ቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:38

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

45,600 ሰዎች

“አርባ አምስት ሺህ ስድስት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:42

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

64,400 ሰዎች

“ስድሳ አራት ሺህ አራት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:44

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:48

አጠቃላይ መረጃ

የእሥራኤል መሪዎች ከ20 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎችን ከትውልዳቸውና ከነገዳቸው አንፃር እየቆጠሩ ነው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውንና ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

45,400 ሰዎች

“አርባ አምስት ሺህ አራት መቶ ሰዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:51

ሙሉ ቁጥሩ

“አጠቃላይ ቁጥሩ”

601,730

“ስድስት መቶ አንድ ሺህ ሰባት መቶ ሰላሣ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:52

ምድሪቱ ትካፈላለች

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“መሬቱን ማከፋፈል አለባችሁ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እነዚህ ሰዎች

ይሄ የሚያመለክተው ከኦሪት ዘኁልቁ 26፡5 ጀምሮ በየወገናቸው የተቆጠሩትን ሁሉ ነው፡፡

በስማቸው ቁጥር መሠረት

“በእያንዳንዱ ወገን ውስጥ ባለው የሕዝብ ቁጥር መሠረት”

Numbers 26:54

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

የበለጠ ርስት ሥጣቸው

በዚህ ምንባብ ወስጥ “ርስት”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የተወረሰውን መሬት ነው፡፡የዓረፍተ ነገሩ ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“እንደ ርስት አድርገህ የበለጠ ትሰጣቸዋለህ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የተቆጠሩት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእሥራኤል መሪዎች የቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሪቱ መከፋፈል ይኖርባታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ምድሪቱን ማከፋፈል አለባችሁ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በዕጣ

“ዕጣ በመጣል”

ይከፋፈላል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ታከፋፍሉታላችሁ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእነርሱ ማከፋፈል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“መሬቱን ለእነርሱ ማከፋፈል ይኖርባችኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:57

አጠቃላይ መረጃ

ይሄ የሌዋውያን ነገድ የሥም ዝርዝር ነው፡፡ምንም መሬት ባለመቀበላቸው ምክኒያት ሙሴ ሌዋውያንን ለብቻቸው ቆጠራቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

በየነገዳቸው ተቆጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“መሪዎቹ በየነገዳቸው ቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ጌድሶን…ቀዓት…ሜራሪ..እንበረም

የእነዚህን ሰዎች ሥም በዘኁልቁ 3፡17-19 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ለእንበረም ልጆች ወለደችለት

“እርሷና እንበረም ልጆች ነበሯቸው”

Numbers 26:60

ናዳብ…አብዮድ…ኢታምር

የእነዚህን ሰዎች ሥም በዘኁልቁ 3፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት የሌለውን እሳት አቀረቡ

እዚህ ላይ“እሣት” የሚለው ቃል የሚያመለክተው “የሚቃጠል መሥዋዕትን”ነው፡፡ተመሳሳይ የሆነውን ሐረግ በዘኁልቁ 3፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“እርሱ ባልተቀበለው ሁኔታ የሚቃጠል መሥዋዕትን አቀረቡ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የተቆጠሩት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“መሪዎቹ የቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ሃያ ሶስት ሺህ

“23,000”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ከአንድ ወር ጀምሮ ከዚያ በላይ ያሉ

“አንድ ወርና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያለው”

ርሰት አልተሰጣቸውም ነበር

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡እዚህ ላይ “ርስት”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የተወረሰውን መሬት ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ምንም ዓይነት መሬት በርስትነት እአይሰጣቸውም አለ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:63

በሙሴና በካህኑ አልዓዛር የተቆጠሩት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴና ካህኑ አልዓዛር የቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አንድም ሰው አልነበረም

“ሰዎች አልነበሩም”

በሙሴና በካህኑ አሮን የተቆጠሩት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሙሴና ካህኑ አሮን የቆጠሯቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤልን ልጆች በቆጠሯቸው ጊዜ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእሥራኤልን ትውልድ በቆጠሩበት ወቅት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 26:65

ከእነርሱ አንድ ሰው ስንኳ አልቀረም

“እነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በሲና ምድረ በዳ ተቆጥረው የነበሩትን ሰዎች ሁሉ ነው፡፡ይሄ በአዎንታዊ መለኩ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እስከ አሁን ድረስ በሕይወት ያሉት ሰዎች”(ድርብ አሉታውያን)

የዮፎኒ ልጅ

ዮፎኒየካሌብ አባት ነበር፡፡ይህንን በዘኁልቁ 13፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

የነዌ ልጅ

ነዌ የኢያሱ አባት ነበር፡፡ይህንን በዘኁልቁ 11፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡


Chapter 27

1 ከዚያ ከዮሴፍ ልጅ ለምናሴ ነገድ የአፌር ወንድ ልጅ የገለአድ ወንድ ልጅ የማኪር ወንድ ልጅ የምናሴ ወንድ ልጅ የሰለጵዓድ ሴት ልጆች ወደ ሙሴ መጡ የሰለዓድ ሴት ልጆች ስሞች እነዚህ ነበሩ፡፡ ማህላህ፣ ኑዓ፣ ዔግላ፣ ሚልካና ቲርጳ፡፡ 2 እነርሱም በሙሴ፣ በካህኑ አልዓዛር፣ በመሪዋች፣ እና በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ በመላው ማህበረሰቡ ፊት ቆሙ፡፡ እንዲህም አሉ፣ 3 “አባታችን በምድረበዳው ሞተ፡፡ እርሱ በቆሬ አመጽ በያህዌ ፊት አምጸው በአንድነት ከተነሱት መሀል አልነበረም፡፡ የሞተው በራሱ ኃጢአት ነበር፣ አባታችን የሞተው በራሱ ኃጢአት ምክንያት ነበር፡፡ 4 ስለምን ወንድ ልጅ ስለሌለው የአባታችን ስም ከጎሳው አባላት ተለይቶ ይጠፋል? በአባታችን ቤተዘመዶች መሀል መሬት ስጠን፡፡” 5 ሙሴ ጉዳያቸውን ያህዌ ፊት አቀረበ፡፡ 6 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው፣ 7 ”የሰለጰዓድ ሴት ልጆች የተናገሩት ትክክል ነው፡፡ በአባታቸው ዘመዶች መሃል በእርግጥ ርስት አድርገህ መሬት ስጣቸው፣ ደግሞም የአባታቸው ርስት ወደ እነርሱ መተላፉን አረጋግጥ፡፡ 8 ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‘አንድ ሰው ወንድ ልጅ ሳይኖው ቢሞት፣ ርስቱ ወደ ሴት ልጁ እንዲተላፍ አድርጉ፡፡ 9 ሴት ልጅ ባይኖረው፣ ርስቱን ለወንድሞቹ ስጡ፡፡ 10 ወንድሞች ባይኖት፣ ርስቱን ለአባቱ ወንድሞች ስጡ፡፡ 11 አባቱ ወንድሞች ባይኖሩት ርስቱን በጎሳው ውስጥ ለቅርብ ዘመዱ ስጡ፣ ያም ሰው ይውሰደው፡፡ ይህም ያህዌ እንዳዘዘኝ፣ ለእስራኤል ህዝብ በአዋጅ የፀና ህግ ይሆናል፡፡’” 12 “ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ “ወደ ዓባሪም ተራሮች ወጥተህ ለእስራኤል ህዝብ የሰጠሁትን ምድር ተመልከት፡፡ 13 ከተመለከትካት በኋላ፣ አንተም ደግሞ ወደ ሰዎችህ እንደ ወንድምህ አሮን ሁሉ ትሰበስባለህ፡፡ 14 ይህ ይሆናል፤ ምክንያቱም በጺን ምድረበዳ እናንተ ሁለታችሁ በትእዛዛቶቼ ላይ አምጻችኋል፡፡ በዚያ፣ ውሃው ከአለቱ ሲፈስስ በቁጣህ ምክንያት በመላው ማህበረሰብ ዐይኖች ፊት እኔን በቅድስና ማክበር አልቻልክም፡፡” ይህ በጺን ምድረበዳ በቃዴስ የሚገኝ የመሪባ ውሃ ነው፡፡ 15 ከዚያ ሙሴ ለያህዌ እንዲህ አለ፣ 16 “የሰዎች ሁሉ መንፈስ አምላክ ያህዌ ሆይ፣ በዚህ ማህበረሰብ ላይ መሪ የሚሆን ሰው ሹም፣ 17 በፊታቸው የሚወጣና የሚገባ ሰው፣ እየመራ የሚያስወጣቸውና የሚያስገባቸው፣ ህዝብህ እረኛ እንደሌላቸው በጎች እንዳይሆን ሰው ሹምለት፡፡” 18 ያህዌ ሙሴን፣ “የእኔ መንፈስ የሚኖርበትን፣ የነዌን ልጅ ኢያሱን ውሰድና እጆችህን በእርሱ ላይ ጫን፡፡ 19 በካህኑ አልዓዛር ፊትና በመላው ማህበረሰብ ፊት አቁመህ እንዲመራቸው በፊታቸው ሹመው፡፡ 20 ከአንተ ስልጣን በእርሱ ላይ አድርግ፣ ስለዚህም መላው የእስራኤል ማህበረሰብ እርሱን ይታዘዙታል፡፡ 21 እርሱም በኡሪም በመጠየቅ ፍቃዴን ለማወቅ በካህኑ አልዓዛር ፊት ይሄዳል፡፡ ህዝቡ፣ እርሱና ከእርሱ ጋር መላው የእስራኤል ሰዎች፣ መላውም ማህበረሰብ የሚወጣውና የሚገባው በእርሱ ትዕዛዝ ይሆናል፡፡ 22 ስለዚህም ሙሴ ያህዌ እርሱን እንዳዘዘው አደረገ፡፡ ኢያሱን ወስዶ በካህኑ አልዓዛርና በመላው ማህበር ፊት አቆመው፡፡ 23 ያህዌ እንዲያደርግ እንዳዘዘው ሁሉ እጆቹን በላዩ ጫነና እንዲመራ ሾመው፡፡



Numbers 27:1

ከዚያም የሰለጰዓድ ሴቶች ልጆች ወደ ሙሴ ቀረቡ ….የዮሴፍ ልጅ

ከዚያም ከዮሴፍ ልጅ ከምናሴ ወገኖች፤የምናሴ ልጅ፤የማኪር ልጅ፤የገለዓድ ልጅ፤የኦፌር ልጅ የሰለጰዓድ ሴቶች ልጆች ወደ ሙሴ ቀረቡ፡፡ይሄ የትውልድን ሐረግ ይናገራል፡፡

ሰለጰዓድ የኦፌር ልጅ …ማህለህ፤ኑዓ፤ዔግላ፤ሚልካ፤ቲርጳ

ይህንን በዘኁልቁ26፡33 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

ገለዓድ….ማኪር

ይህንን በዘኁልቁ 26፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 27:2

ቀረቡ

“የሰለጰዓድ ሴቶች ልጆች ቀረቡ”

በቆሬ ማህበር ውስጥ ሆኖ በእግዚአብሔር ላይ ያመፀ

በቆሬ ማህበር ውስጥ የነበሩት ሰዎች ተሰባሰበው በእግዚአብሔር ላይ አመፁ፡፡እግዚአብሔር ከኃጢአታቸው የተነሣ እንዲሞቱ አደረገ፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“በእግዚአብሔር ላይ ያመፁ የቆሬ ማህበር ተከታዮች በመሆናቸው የሞቱ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በራሱ ኃጢአት

“ከራሱ ኃጢአት የተነሣ”

Numbers 27:4

ወንድ ልጅ ባይኖረው የአባታችን ስም ከወገኑ መካከል ለምን ይጠፋል?

በዚያን ዘመን መሬት የመውረስ ሥልጣን የነበረው ወንድ ልጅ ብቻ ነበር፡፡ሴቶቹ ይህንን ጥያቄ የጠየቁት ውርሱን በመውረስ የዘር ሐረጉ እንዲቀጥል ለማስቻል ነበር፡፡ይሄ እንደ መግለጫ ሊፃፍ ይችላል፡፡“አባታችን ወንድ ልጅ ስለሌለው ብቻ የአባታችንን ሥም ከነገድ አባልነቱ ልትፍቁት አይገባም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በአባታችን ወንድሞች መካከል ርስትን ስጠን

ይሄ የአባታቸው ዘመዶች በወረሱት ርሰት አካባቢ የሚወርሱት ርስት ይሰጣቸው ዘንድ ያቀረቡት ጥያቄ ነው፡፡የዚህ ፍቺ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“የአባታችን ዘመዶች ባሉበት ሥፍራ ላይ ርስትን ሥጠን”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 27:6

በአባታቸው ዘመዶች መካከል

ይሄ ማለት የአባታቸው ዘመዶች በወረሱት ርሰት አካባቢ የሚወርሱት ርስት ይሰጣቸዋልማለት ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“የአባታቸው ወንድሞች ወደሚኖሩበት”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 27:9

አጠቃላይ መረጃ

ይሄ ክስተት አንድ ሰው ወንድ ልጅ የማይኖረው ከሆነ መሬቱን ማን ሊወርስ እንደሚችል ለመወሰን የእግዚአብሔር ሕግ እንዲወጣ ምክኒያት ሆኗል፡፡

ለእሥራኤል ልጆች ሥርዓትና ፍርድ ይሁን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእሥራኤል ሕዝብ ሁሉ የሚታዘዘው ሕግ ይሁን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እኔን አዘዘኝ

እዚህ ላይ“እኔን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴን ነው፡፡

Numbers 27:12

ዓባሪም ተራራ

እነዚህ በሞአብ ውስጥ የሚገኙ የተያያዙ ተራራዎች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእሥራኤል ልጆች የሰጠኋትን

እዚህ ላይ እግዚአብሔር ለእሥራኤላውያን እየሰጠ ያለውን ምድር ልክ ሰጥቶ እንደጨረሰ ዓይነት አድርጎ ይናገራል፡፡በዚህ መልኩ የሚናገርበት ምክኒያት የሚሰጣቸው ስለመሆኑ አስረግጦ ለማሳሰብ ነው፡፡“ለእሥራኤል ሕዝብ የምሰጠውን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አንተ ደግሞ ወደ ወገኖችህ ትከማቻለህ

ይሄ ጨዋ የሆነ አነጋገር ሲሆን ትርጉሙም ሙሴ እንደሚሞትና መንፈሱም አባቶቹ ወዳሉበት የሚሄድ መሆኑን ነው፡፡“መሞት አለብህ”(የጨዋ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እንደ ወንድምህ እንደ አሮን

አሮን መሞቱ የታወቀ ነገር ቢሆንም የበለጠ ግን ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡“ታላቅ ወንድምህ አሮን እንደሞተ”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

ሁለታችሁም አምፃችኋል

ይሄ የሚያመለክተው ሙሴና አሮንን ነው፡፡

የጺን ምድረ በዳ

ይህንንዓረፍተ ነገርበዘኁልቁ 13፡21 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በቁጣህ ውኃው ከዓለት ውስጥ በፈለቀበት ወቅት

ይሄ የሚያመለክተው እግዚአብሔር ተአምራታዊ በሆነ መልኩ ውኃን ባወጣበት ወቅት ነበር፡፡እግዚአብሔር ድንጋዩን እንዲናገረው ሙሴን አዘዘው፡፡በዚህ ምትክ ግን በሕዝቡ ከመናደዱ የተነሣ ዓለቱን በበትሩ መታው፡፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አልቀደሳችሁኝምና

“ቅዱስ እንደሆንኩ አላሰባችሁም”

በማህበሩ ሁሉ ፊት

እዚህ ላይ ያዩትን ነገር አፅንዖት ለመስጠት ሰዎች የሚወከሉት “በዓይኖቻቸው”ነው፡፡“ማህበሩ ሁሉ ባለበት ፊት”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

የመሪባ ውኃ

ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 20፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 27:15

የሥጋ ሁሉ መንፈስ አምላክ እግዚአብሔር

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/እዚህ ላይ “መንፈስ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሕዝብን ሁሉ ነው፡፡“የሰው ዘር ሁሉ የበላይ የሆነው እግዚአብሔር”ወይም 2/“መንፈስ”የሚለው ቃልየሚያመለክተው እግዚአብሔር ለሰው ሁሉ ሕይወትንና ትንፋሽን መሥጠቱን ነው፡፡ “ለሰው ሁሉ ትንፋሽን የሚሰጠው እግዚአብሔር”ወይም“ለሰው ሁሉ ሕይወትን የሚሰጠው እግዚአብሔር”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

በማህበሩ ላይ

በተወሰኑ ሰዎች “ላይ”መሆን ማለት እነርሱን ለመምራት ሥልጣን መያዝ ማለት ነው፡፡“ማህበሩን የሚመራ ሰው”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በፊታቸው የሚወጣውን፤በፊታቸውም የሚገባውን፤የሚያስወጣቸውንም የሚያስገባቸውንም ሰው

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ሕዝቡን የሚመራና በጦርነትም ወቅት ሠራዊቱን የሚመራ ማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔር መንጋ እረኛ እንደሌለው መንጋ እንዳይሆን

ይሄ ንፅፅር ሲሆን የዚህ ሃሣብ ትርጉም ሕዝቡ መሪ የማይኖረው ከሆነ የተቅበዘበዘና ደካማ ይሆናል ማለት ነው፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 27:18

መንፈሴ የሚኖርበትን የነዌን ልጅ ኢያሱን ውሰድ

የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት ሲል ኢያሱ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ የሚከተልና የሚታዘዝ ነው ማለቱ ነው፡፡

እጅህን በላዩ ጫንበት

ይሄ አንድን ሰው ለእግዚአብሔር ለመለየት የሚካሄድ ሥርዓት ነው፡፡“እርሱን ለመቀባት እጅህን በላዩ ላይ ጫንበት”(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

መሪያቸው ይሆን ዘንድ እነርሱ እያዩ እዘዘው

እዚህ ላይ ያዩትን ነገር አፅንዖት ለመስጠት ሰዎች የሚወከሉት “በዓይኖቻቸው”ነው፡፡“የእሥራኤልን ሕዝብ ይመራ ዘንድ በሁሉ ፊት ኢያሱን እዘዘው”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 27:20

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ለሙሴና ለኢያሱ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ከክብርህ አኑርበት

እዚሀ ላይ እግዚአብሔር ልክ በላዩ እንደሚደረግ ነገር ወይም አልባሳት ለኢያሱ ክብሩን እንዲያኖርበት ይናገረዋል፡፡“ከሥልጣንህ የተወሰነውን ክፍል መሥጠት ይኖርብሃል”ወይም “ሰዎች ማድረግ የሚኖርባቸውን ነገር እርሱ ይወስን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ኡሪም

ይሄ የተቀደሰ ድንጋይ ሲሆን ሊቀ ካህኑ በደረቱ ላይ የሚያደርገው ነገር ነው፡በእግዚአብሔር ነገር ላይ ውሳኔ ለመሥጠት የሚጠቀምበት ነገር ነበር፡፡(የማይታወቁትን መተርጎም የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል ማህበር ሁሉ በቃሉ ይውጡ በቃሉም ይግቡ

ይሄ ማለት ኢያሱ የእሥራኤልን ማህበር እንቅስቃሴዎች የማዘዝ ሥልጣን ይኖረዋል ማለት ነው፡፡“መውታጣ”እና “መግባት”የሚሉት ቃላት በእንቅስቃሴያቸው ላይ ሙሉ ሥልጣን እንዳለው አፅንዖት የሚሰጡ ሁለት ተቃራኒ የሆኑ ትዕዛዛቶች ናቸው፡፡“የማህበሩን እንቅስቃሴ ይመራል” (ሆን ብሎ አጋኖ መናገር የሚለውን ይመልከቱ)

እርሱ ከእርሱም ጋር የእሥራኤል ልጆች ማህበር ሁሉ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን በጥምረት የቀረቡበት ምክኒያት ለጉዳዩ አፅንኦት ለመሥጠት ሲባል ነው፡፡“እርሱና የእሥራኤል ሕዝብ ሁሉ”(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 27:22

ፊት አቆመው

“በማህበሩ ፊት እንዲቆም አዘዘው”

እርሱ እጁን በላዩ ላይ ጭኖ መሪ ይሆን ዘንድ እርሱን አዘዘው

“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴን ሲሁን “እርሱ”የሚለው ቃል ደግሞ የሚያመለክተው ኢያሱን ነው፡፡

እጁን በላዩ ላይ ጫነበት

እጅ መጫን አንድን ሰው ለተለየ የእግዚአብሔር አገልግሎት ለመለየት የሚደረግ ሥርዓት ነው፡፡(ተምሣሌታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

መምራት

ግልፅ የሆነውንና ሰዎችን የመምራትን ጉዳይ የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡“ሰዎችን መምራት”ወይም“የእሥራኤላውያን መሪ መሆን”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር እርሱን ባዘዘው መሠረት

እዚህ ላይ “እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሴን ነው፡፡


Chapter 28

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 ”የእስራኤል ሰዎችን እንዲህ ብለህ እዘዛቸው፣ ‘በወቅቱ ለእኔ መስዋዕቶችን አቅርቡ፣ ለእኔ ጣፋጭ መዓዛ ያለው በእሳት የተበጀ መስዋዕት ለእኔ አቅርቡልኝ፡፡’ 3 ደግሞም እንዲህ በላቸው፣ ‘ይህ ለያህዌ የምታቀርቡት የእሳት መስዋዕት ነው፡፡ ነውር የሌለበት የአንድ አመት ጠቦት፣ እንደ መደበኛ መስዋዕት በእያንዳንዱ ቀን ሁለት ጠቦቶች አቅርቡ፡፡ 4 አንዱን ጠቦት በማለዳ ታቀርባላችሁ፣ ሌላውን ጠቦት በምሽት ታቀርባላችሁ፡፡ 5 በተጠለለ የኢን አንድ አራተኛ ዘይት የተለወሰ የአፍ አንድ አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን አድርጋችሁ አቅርቡ፡፡ 6 ይህ በሲና ተራራ የተደነገገ ለያህዌ የሚቀርብ በእሳት የተዘጋጀ መልካም መዓዛ ያለው መደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት ነው፡፡ 7 ከዚህ ጋር የሚቀርበው የመጠጥ መስዋዕት ለአንዱ ጠቦት የኢን አንድ አራተኛ ይሁን፡፡ በተቀደሰው ስፍራ ለያህዌ የመጠጥ ስጦታ አፍስሱ፡፡ 8 ሌላውን ጠቦት ከሌላ የእህል ቁርባን ጋር በማለዳ ባቀረባችሁት መስዋዕት አይነት በምሽት አቅርቡ፡፡ ከዚህ ጋር ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ እንዲሆን በእሳት የተዘጋጀ ሌላ የመጠጥ መስዋዕትም አቅርቡ፡፡ 9 በሰንበት ቀን ነውር የሌላቸው ሁለት የአንድ አመት ጠቦቶች፣ እና በዘይት የተለወሰ የኢፍ ሁለት አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን አድርጋችሁ ከመጠጥ መስዋዕት ጋር አቅርቡ፡፡ 10 ይህ ከመደበኛው የሚቃጠል መስዋዕትና ከዚህ ጋር ከሚቀርበው የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ በየሰንበቱ የሚቃጠል መስዋዕት እንዲሆን ነው፡፡ 11 በየወሩ መጀመሪያ፣ ለያህዌ የሚቃጠል መስዋዕት አቅርቡ፡፡ ሁለት ወይፈኖች፣ አንድ አውራ በግ እና ነውር የሌለባቸው ሰባት ወንድ የበግ ጠቦት መስዋዕት አድርጋችሁ አቅረቡ፡፡ 12 ለእያንዳዱ ወይፈን በዘይት የተለወሰ የኢፍ ሶስት አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን አቅርቡ፣ ደግሞም ከአውራ በጉ ጋር በዘይት የተለወሰ የኢፍ ሁለት አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን አቅርቡ፡፡ 13 እንደዚሁም ለእያንዳንዱ ጠቦት የኢፍ አንድ አስረኛ በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን አቅርቡ፡፡ ይህ ለያህዌ የሚቀርብ በእሳት የተዘጋጀ መልካም መዓዛ የሚሰጥ የሚቃጠል መስዋዕት የሚሆን ነው፡፡ 14 የሰዎች የመጠጥ ቁርባን ላንድ ኮርማ በሬ የኢን ግማሽ ወይን ጠጅ ይሁን፣ ከአውራ በጉ ጋር የኢን አንድ ሶስተኛ፣ ለአንድ ጠቦት በግ የኢን አንድ አራተኛ ወይን ጠጅ ይሁን፡፡ ይህ አመቱን በሙሉ በእያንዳንዱ ወር የሚቃጠል መስዋዕት ነው፡፡ 15 ለያህዌ አንድ ወንድ ፍየል የኃጢአት መስዋዕት መቅረብ አለበት፡፡ ይህ ከመደበኛው የሚቃጠል መስዋዕትና ከዚህ ጋር ከሚቀርብ የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ነው፡፡ 16 በመጀመሪያው ወር፣ በወሩ በአስራ አራተኛው ቀን የያህዌ ፋሲካ ይውላል፡፡ 17 በዚህ ወር የአስራ አምስተኛው ቀን ክብረ በዓል ይሆናል፡፡ ለሰባት ቀናት እርሾ የሌለበት ቂጣ ይበላል፡፡ 18 በመጀመሪያው ቀን ያህዌን ለማክበር ቅዱስ ጉባኤ ይደረጋል፡፡ በዚያ ቀን የዘወትር ሥራችሁን አትሰሩም፡፡ 19 ሆኖም ለያህዌ በእሳት የተዘጋጀ የሚቃጠል መስዋዕት ስጦታ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ፡፡ ሁለት ወይፈኖች፣ አንድ አውራ በግ፣ እና ነውር የሌለባቸው የአንድ አመት ሰባት ወንድ የበግ ጠቦቶች ታቀርባላችሁ፡፡ 20 ከወይፈኑ ጋር በዘይት የተለወሰ የኢን ሶስት አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን፣ ከአውራ በግ ጋር የኢን ሁለት አስረኛ መልካም ዱቄት የእህል ቁርባን አቅርቡ፡፡ 21 ከእያንዳንዳቸው ከሰባቱ ጠቦቶች ጋር፣ በዘይት የተለወሰ የኢፍ አንድ አስረኛ መልካም ዱቄት አቅርቡ፣ 22 እንዲሁም አንድ ወንድ ፍየል ለኃጢአት መስዋዕት ለማስተሰርያ አቅርቡ፡፡ 23 እነዚህን በየጠዋቱ ከሚያስፈልገው መደበኛው የሚቃጠል መስዋዕት በተጨማሪ አቅርቡ፡፡ 24 እዚህ እንደ ተገለፀው፣ እነዚህን መስዋዕቶች በየቀኑ ማቅረብ አለባችሁ፣ በፈሲካ ሳምንት፣ በእሳት የተዘጋጀው የምግብ መስዋዕት ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ ይቅረብ፡፡ ይህ ከመደበኛው የሚቃጠል መስዋዕትና ከዚህ ጋር ከሚቀርበው የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ መቅረብ አለበት፡፡ 25 በሰባተኛው ቀን ያህዌን ለማክበር የተቀደሰ ጉባኤ ይኑራችሁ፣ ደግሞም በዚያ ቀን የየዕለት ተግባራችሁን አታከናውኑ፡፡ 26 እንደዚሁም በበኩራት ፍሬ ቀን፣ በክብረ በዓላችሁ ሳምንታት የአዲስ እህል ስጦታ ለያህዌ ስታቀርቡ፣ ያህዌን ለማክበር የተቀደሰ ጉባኤ ይኑራችሁ፤ ደግሞም በዚያ ቀን የተለመደ የየዕለት ተግባራችሁን አትስሩ፡፡ 27 ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ የሚቃጠል መስዋዕት አቅርቡ፡፡ ሁለት ወይፈኖች፣ አንድ አውራ በግ፣ እና ሰባት የአንድ አመት ጠቦት በጎች አቅርቡ፡፡ 28 ከእነዚህ ጋር እነዚህን የእህል ቁርባን አቅርቡ በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት፣ ለእያንዳንዱ ወይፈን የኢፍ ሶስት አስረኛ በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት፣ እና ለአውራ በጉ ሁለት አስረኛ የእህለ ቁርባን አቅርቡ 29 የኢፍ አንድ አስረኛ በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት ለእያንዳንዳቸው ሰባት ጠቦቶች አቅርቡ፣ 30 ደግሞም አንድ ወንድ ፍየል ለኃጢአታችሁ ማስተሰርያ አቅርቡ፡፡ 31 ነውር የሌለባቸውን እነዚያን እንስሳት ከመጠጥ ቁርባናቸው ጋር ስታቀርቡ ይህ ከመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕትና ከዚህ ጋር ከሚቀርበው የእህል ቁርባን በተጨማሪ መሆን አለበት፡፡’”



Numbers 28:1

በየጊዜው

“እኔ በመረጥኩኩት ቀን”

በእሳት የተደረገውን ቁርባኔን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በመሠዊያው ላይ የምታቀርቡት መብል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእኔ ጣፋጭ ሽታ

“የምወደውን ሽታ”

Numbers 28:3

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ህዝቡ ምን ማድረግ እንዳለበት ለሙሴ መንገሩን ይቀጥላል፡፡

በእሣት የሚደረግ ቁርባን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእሳት የሚቃጠል ቁርባን”ወይም “በመሥዋዕቱ ላይ በእሣት ያቃጠላችሁት ቁርባን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የተለወሰ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ከ..ጋር የለወሳችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የኢፍ መሥፈሪያ አሥረኛ እጅ

“አሥረኛ እጅ”ማለት አሥር አኩል ከሆኑ ነገሮች ውስጥ አንዱ ክፍል ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ሁለት ሊትሮች”ወይም “የኢፍ መስፈሪያ አንድ አሥረኛ”(ይሄ ሁለት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

የኢን መሥፈሪያ አንድ አራተኛ እጅ

“አራተኛ እጅ”ማለት አራት አኩል ከሆኑ ነገሮች ውስጥ አንዱ ክፍል ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“አንድ ሊትር”ወይም “የኢን መስፈሪያ አንድ አራተኛ”(ይሄ አንድ ሊትር ያህል ይሆናል) (ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

በተጠለለ ዘይት

“የተወቀጠ ዘይት”ወይም “ንፁህ ወይራ ዘይት”ይሄ የሚያመለክተው ከወይራ ተወቅጦ የወጣን ዘይት ነው፡፡

Numbers 28:6

በሲና ተራራ ላይ የታዘዘ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ ያዘዘው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሣት የቀረበ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእሣት ላይ ያቃጠላችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የኢን መሥፈሪያ አንድ አራተኛ እጅ

“አራተኛ እጅ”ማለት አራት አኩል ከሆኑ ነገሮች ውስጥ አንዱ ክፍል ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“አንድ ሊትር”ወይም “የኢን መስፈሪያ አንድ አራተኛ”(ይሄ አንድ ሊትር ያህል ይሆናል) (ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

በመቅደሱ ውስጥ ለእግዚአብሔር ለመጠጥ ቁርባን መጠጥ ታፈስሳለህ

ይሄ ዓረፍተ ነገር የሚያሣየው ከበግ ጠቦቱ ጋር አብሮ የሚቀርበውን የመጠጥ ቁርባን ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ጠንካራ የሆነ የመጠጥ ቁርባን ሊሆን የሚገባው ሲሆን በእግዚአብሔር መቅደስ ውስጥ ልታፈስሱት ይገባል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በፊት እንዳቀረብከው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንተ ያቀረብከው ዓይነት”

Numbers 28:9

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

ከመሥፈሪያው ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች ሁለቱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“አራት ሊትር ተኩል”ወይም “ከመሥፈሪያው ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”(አራት ሊትር ተኩል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሳችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእርሱ ጋር የመጠጥ ቁርባን

ብዙ ቁርባኖች አብሮ የመጠጥ ቁርባን እንዲቀርብ የሚጠይቁ ናቸው፡፡የዚህ ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“የመጠጥ ቁርባንም አብሮ ይቀርባል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 28:11

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

ከመሥፈሪያው አሥር እጅ ሶስት እጅ

“ከአሥር እጅ ሶስት እጅ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች ሶስቱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ስድስት ሊትር”ወይም “ከመሥፈሪያው ከአሥር እጅ ሶስት እጅ”(ስድስት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሳችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ ሁለት እጅ መልካም ዱቄት

“ኢፍ”የሚለው ቃል ግልፅ ቢሆንም የበለጠ ሊብራራ ግን ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ ሁለቱ ማለት ነው፡፡“አራት ተኩል ሊትር መልካም ዱቄት”ወይም “ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን፤ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከመሥፈሪያው አንድ አሥረኛ እጅ

“አንድ አሥረኛ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች አንዱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ሁለት ሊትር”ወይም “ከመሥፈሪያው አሥረኛ እጅ”(ሁለት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

በእሣት የቀረበ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእሣት ላይ ያቃጠላችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 28:14

የኢን ግማሽ

“ግማሽ”ማለት ሁለት እኩል ከሆኑ ክፍሎች ውስጥ አንደኛው ክፍል ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ሁለት ሊትር”ወይም “የኢን ግማሽ”(ሁለት ሊትር)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

የኢን ሢሶ

“የኢን አንድ ሶስተኛ”አንድ ሶስተኛ ማለት ሶስት እኩል ከሆኑ ክፍሎች ውስጥ አንደኛው ክፍል ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“1.2 ሊትር”ወይም “አንድ ሊትርና አንድ አምስተኛ ሊትር”(ሁለት ሊትር ማለት ነው)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

የኢን አራተኛ እጅ

“አራተኛ እጅ”ማለት አራት እኩል ከሆኑ ክፍሎች ውስጥ አንደኛው ክፍል ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“አንድ ሊትር”ወይም “የኢን አራተኛ እጅ”(አንድ ሊትር ያህል የሆነ)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር አንድ አውራ ፍየል ይቀርባል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡ለኃጢአት መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል ለእግዚአብሔር ታቀርባላችሁ፡፡(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 28:16

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በመጀመሪያው ወር ከወሩም በአሥራ አራተኛው ቀን….ከዚህም ወር በአሥራ አምስተኛው ቀን

“በመጀሪያው ወር በወሩ በ14ኛው ቀን…በዚሁ ወር በ15ኛው ቀን” “ይሄ የሚያመለክተው የመጀመሪያውን የዕብራውያንን ወር ነው” (የዕብራውያን ወራትናተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔር ፋሲካ ነው

“የእግዚአብሔርን ፋሲካ ልታከብሩት ይገባል”

በዓል ይሆናል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዓል ልታደርጉ ይገባል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እርሾ የሌለው ቂጣ መበላት ይኖርበታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እርሾ የሌለው ቂጣ ልትበሉ ይገባል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በመጀመሪያው ቀን

ይሄ የሚያመለክተው የበዓሉን የመጀመሪያ ዕለት ነው፡፡ይሄ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“በበዓሉ በ1ኛው ቀን” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን ለማክበር የተቀደሰ ጉባዔ መደረግ ይኖርበታል

“እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማክበር መሰብሰብ ይኖርባችኋል፡፡” “የተቀደሰ ጉባዔ”የሚለው ሐረግ ሰዎች ተሰብስበው እግዚአብሔርን ሲያመልኩ ማለት ነው፡፡እግዚአብሔርን ማምለክ የተቀደሰ ክስተት ነው፡፡

Numbers 28:19

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በእሣት የተደረገውን የሚቃጠለውን መሥዋዕት ታቀርባላችሁ

“የሚቃጠል”የሚለው ቃል በፍዝ መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በመሠዊያው ላይ የሚቃጠል መሥዋዕት ማቅረብ ይኖርባችኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከመሥፈሪያው ከአሥር እጅ ሶስት እጅ

“ከአሥር እጅ ሶስት እጅ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች ሶስቱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ስድስት ሊትር”ወይም “ከመሥፈሪያው ከአሥር እጅ ሶስት እጅ”(ስድስት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሳችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ ሁለቱ ማለት ነው፡፡“አራት ተኩል ሊትር የሆነ መልካም ዱቄት”ወይም “ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን፤ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከመሥፈሪያው አንድ አሥረኛ እጅ

“አንድ አሥረኛ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች አንዱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ሁለት ሊትር”ወይም “ከመሥፈሪያውአንድ አሥረኛ እጅ”(ሁለት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

መሥዋዕትን ማቅረብ

x

Numbers 28:23

ዘወትር ማልዶ ከሚቀርበው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በየማለዳው እንዲቀርብለት ከሚፈልገው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እዚህ በተገለፀው መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እኔ እግዚአብሔር እዚህ በገለፅኩት መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በእሣት የሚደረገውን የመብል ቁርባን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የመብሉን ቁርባን በመሠዊያው ላይ ማቃጠል ይኖርባችኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር የሚሆን ጣፋጭ ሽታ

“ለእግዚአብሔር እንደ ጣፋጭ ሽታ”

መሥዋዕት መደረግ ይኖርበታል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ልትሰውት ይገባል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን ለማክበር የተቀደሰ ጉባዔ መደረግ ይኖርበታል

“እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማክበር መሰብሰብ ይኖርባችኋል፡፡” “የተቀደሰ ጉባዔ”የሚለው ሐረግ ሰዎች ተሰብስበው እግዚአብሔርን ሲያመልኩ ማለት ነው፡፡እግዚአብሔርን ማምለክ የተቀደሰ ክስተት ነው፡፡

Numbers 28:26

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በበኩራት ቀን

በበኩራት ቀንሲባልዕለቱን ነው፡፡“ይሄ የሚያመለክተው በዓሉ በሚከበርበት ሣምንታት ውስጥ ለእግዚአብሔር የእህል ቁርባን የሚያቀርቡበትን ዕለት ነው፡፡

እግዚአብሔርን ለማክበር የተቀደሰ ጉባዔ መደረግ ይኖርበታል

“እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማክበር መሰብሰብ ይኖርባችኋል፡፡” “የተቀደሰ ጉባዔ”የሚለው ሐረግ ሰዎች ተሰብስበው እግዚአብሔርን ሲያመልኩ ማለት ነው፡፡እግዚአብሔርን ማምለክ የተቀደሰ ሁኔታ ነው፡፡

በዘይት የተለወሰ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሳችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ ሁለቱ ማለት ነው፡፡“አራት ተኩል ሊትር የሆነ መልካም ዱቄት”ወይም “ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን፤ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከመሥፈሪያው ሶስትአሥረኛ እጅ

“ሶስት አሥረኛ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች ሶስቱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ስድስት ሊትር”ወይም “የኢፍ መሥፈሪያሶስት አሥረኛ”(ስድስት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ ሁለቱ ማለት ነው፡፡“አራት ተኩል ሊትር የሆነ መልካም ዱቄት”ወይም “ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን፤ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 28:29

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

ከመሥፈሪያው አንድ አሥረኛ እጅ

“አንድ አሥረኛ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች አንዱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ሁለት ሊትር”ወይም “ከመሥፈሪያው አንድ አሥረኛ እጅ”(ሁለት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እናንተ በዘይት የምትለውሱት መልካም ዱቄት” (ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

መሥዋዕትን ማቅረብ

“መሥዋዕት ማቅረብ”የሚለው ሐረግ “መሰዋት”በሚለው ሥም ሊገለፅ ይችላል፡፡(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

የእነርሱን የመጠጥ ቁርባን

“የእነርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እያንዳንዱ እንስሳ በሚሰዋበት ወቅት አብረው መቅረብ የሚገባቸውን የመጠጥ ቁርባኖችን ነው፡፡“ከአነርሱ ጋር አብረው የሚቀርቡት የመጠጥ ቁርባኖች”ወይም “የሚያጅቧቸው የመጠጥ ቁርባኖች”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 29

1 ”በሰባተኛው ወር፣ በወሩ በመጀመሪያው ቀን፣ ያህዌን ለማክበር የተቀደሰ ጉባኤ አድርጉ፡፡ በዚያ ቀን የተለመደውን የዕለት ተግባራችሁን አታከናውኑ፡፡ ይህ ቀን መለከቶችን የምትነፉበት ቀን ይሆናል፡፡ 2 ለያህዌ መልካም መዓዛ የሚሆን የሚቃጠል መስዋዕት አቅርቡ፡፡ አንድ ወይፈን፣ አንድ አውራ በግ፣ እና እያንዳንዳቸው ነውር የሌለባቸው ሰባት የአንድ አመት ጠቦቶች አቅርቡ፡፡ 3 ከእነዚህ ጋር የእህል ቁርባናቸውን፣ በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት አቅርቡ፤ ለወይፈኑ የኢፍ ሶስት አራተኛ፣ ለአውራ በጉ የኢፍ ሁለት አስረኛ 4 እና ለሰባቱ ጠቦቶች ለእያንዳንዳቸው በዘይት የተለወሰ የኢፍ አንድ አስረኛ መልካም ዱቄት አቅርቡ፡፡ 5 ለኃጢአት ማስተስረያ አንድ ወንድ ፍየል አቅርቡ፡፡ 6 በየወሩ መጀመሪያ ከምታደርጉት የተለየ የሚቃጠል መስዋዕትና አብሮ ከሚቀርበው የእህል ቁርባን በተጨማሪ፣ እነዚህን መስዋዕቶች በሰባተኛው ወር አድርጉ፡፡ እነዚህ ከመደበኛው የሚቃጠል መስዋዕት ከእህል ቁርባኑና የመጠጥ ቁርባኖች በተጨማሪ የሚቀርቡ ናቸው፡፡ እነዚህን መስዋዕቶች ስታደርጉ፣ ለያህዌ በእሳት የሚዘጋጀውን መስዋዕት ጣፋጭ መዓዛ ለማቅረብ የተደነገገውን ትፈጽማላችሁ፡፡ 7 በሰባተኛ ወር በአስረኛው ቀን ያህዌን ለማክበር የተቀደሰ ጉባኤ ታደርጋላችሁ፡፡ ራሳችሁን በእግዚአብሔር ፊት ታዋርዳላችሁ በዕለቱ ሥራ አትሰሩም፡፡ 8 ለያህዌ ጣፋጭ ማዐዛ ያለው የሚቃጠል መስዋዕት ታቀርባላችሁ፡፡ አንድ ወይፈን፣ አንድ አውራ በግ፣ እና የአንድ አመት ሰባት ወንድ ጠቦት በጎች ታቀርባላችሁ፡፡ እያንዳንዳቸው ነውር የሌለባቸው ይሁኑ፡፡ 9 ከዚህ ጋር የእህል ቁርባን፤ በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት፣ ለወይፈኑ የኢፍ ሶስት አስረኛ፣ ለአውራ በጉ የኢፍ ሁለት አስረኛ፣ 10 እና ለሰባቱ ጠቦቶች ለእያንዳንዳቸው የኢፍ አንድ አስረኛ ታቀርባላችሁ፡፡ 11 አንድ ወንድ ፍየል ለኃጢአት መስዋዕት ማቅረበ አለባችሁ፡፡ ይህ ለኃጢአት ማስተስረያ፣ ለመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት፣ አብሮት ከሚቀርበው የእህል ቁርባን፣ እና ከእነዚህ ጋር በሚቀርበው የመጠጥ መስዋእቶች በተጨማሪ የሚቀርብ ነው፡፡ 12 በሰባተኛው ወር አስራ አምስተኛው ቀን ያህዌን ለማክበር የተቀደሰ ጉባኤ ታደርጋላችሁ፡፡ በዚያ ቀን የተለመደውን የዕለት ተግባራችሁን አታከናውኑም፣ ደግሞም ለሰባት ቀናት ክብረ በዓሉን ለእርሱ ታደርጋላችሁ፡፡ 13 በእሳት የተዘጋጀ ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ የሚሆን የሚቃጠል መስዋዕት ማቅረብ አለባችሁ፡፡ አስራ ሶስት ወይፈኖች፣ እና የአንድ አመት ዕድሜ ያላቸው አስራ አራት ወንድ ጠቦቶች ማቅረብ አለባችሁ፡፡ እያንዳንችው ነውር የሌለባቸው መሆን አለባቸው፡፡ 14 ከእነዚህ ጋር የእህል ቁርባን፣ ለአስራ ሶስቱም ወይፈኖች ለእያንዳንዳቸው የኢፍ ሶስት አስረኛ፣ ለሁለቱ አውራ በጎች ለእያንዳንዳቸው የኢፍ ሁለት አስረኛ 15 እና ለአስራ አራቱ ጠቦቶች ለእያንዳንዳቸው የኢፍ አንድ አስረኛ፤ በዘይትየተለወሰ መልካም ዱቄት አቅርቡ፡፡ 16 ከመደበኛው የሚቃጠል መስዋዕት፤ ከዚህ ጋር ከሚቀርበው የእህል ቁርባን እና የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 17 በስብሰባው ሁለተኛ ቀን፣ አስራ ሁለት ወይፈኖች፣ ሁለት አውራ በጎች እና አስራ አራት ነውር የሌለባቸው የአንድ አመት ወንድ የበግ ጠቦቶች ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 18 ከእነዚህ ጋር የእህል ቁርባን የመጠጥ ቁርባኖች ለኮርማዎቹ፣ ለአውራ በጎቹ እና ለጠቦቶቹ በተወሰነው ቁጥር መሠረት እንደ ትዕዛዙ ታቀርባላችሁ፡፡ 19 ከመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት፣ አብሮት ከሚቀርበው የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 20 በስብሰባው ሶስተኛ ቀን፣ አስራ አንድ ወይፈኖች ሁለት አውራ በጎች፣ እና አስራ አራት ነውር የሌለባቸው የአንድ አመት ወንድ የበግ ጠቦቶች ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 21 ከእነዚህ ጋር የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባኖች ለኮርማዎቹ፣ ለአውራ በጎቹ፣ እና ለጠቦቶቹ በተወሰነው ቁጥር መሰረት እንደ ትዕዛዙ ታቀርባላችሁ፡፡ 22 ከመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት፣ አብሮ ከሚቀርበው የእህል ቁርባን፣ እና የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 23 በስብሰባው አራተኛ ቀን፣ አስር ወይፈኖች፣ ሁለት አውራ በጎች እና አስራ አራት ነውር የሌለባቸው የአንድ አመት ወንድ የበግ ጠቦቶች ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 24 ከእነዚህ ጋር የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባኖች፣ ለኮርማዎቹ፣ ለአውራ በጎቹ እና ለጠቦቶቹ በተወሰነው ቁጥር መሠረት እንደ ትዕዛዙ ታቀርባላችሁ፡፡ 25 ከመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት፣ አብሮት ከሚቀርበው የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 26 በስብሰባው አምስተኛ ቀን፣ ዘጠኝ ወይፈኖች፣ ሁለት አውራ በጎች፣ እና አስራ አራት ነውር የሌለባቸው የአንድ አመት ወንድ የበግ ጠቦቶች ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 27 ከእነዚህም ጋር የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባኖች ለኮርማዎቹ፣ ለአውራ በጎቹ፣ እና ለጠቦቶቹ፣ በተወሰነው ቁጥር መሠረት እንደ ትዕዛዙ ታቀርባላችሁ፡፡ 28 ከመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት፣ አብሮት ከሚቀርበው የእህል ቁርባን፣ እና የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 29 በስበሰባው ስድስተኛ ቀን ስምንት ወይፈኖች፣ ሁለት አውራ በጎች፣ እና አስራ አራት ነውር የሌለባቸው የአንድ አመት ወንድ የበግ ጠቦቶች ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 30 ከእነዚህ ጋር የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባኖች ለኮርማዎቹ፣ ለአውራ በጎቹ፣ እና ለጠቦቶቹ በተወሰነው ቁጥር መሠረት እንደ ትዕዛዙ ታቀርባላችሁ፡፡ 31 ከመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት፣ አብሮት ከሚቀርበው እህል ቁርባን እና የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረበ አለባችሁ፡፡ 32 በስብሰባው ሰባተኛ ቀን፣ነውር የሌለባቸው፣ ሰባት ወይፈኖች፣ ሁለት አውራ በጎች እና አስራ አራት የአንድ አመት ወንድ የበግ ጠቦቶች ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 33 ከወይፈኖች፣ከአውራ በጎች እና ጠቦቶች ጋር የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባኖች ታቀርባላችሁ፡፡ 34 ከመደበኛው የሚቃጠል መስዋዕትና አብሮት ከሚቀርበው የእህል ቁርባን፣ እንዲሁም ከመጠጥ ቁርባኑ በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 35 በስብሰባው ስምንተኛ ቀን፣ ሌላ የከበረ ጉባኤ ታደርጋላችሁ፡፡ በዚያን ቀን የተለመደ የዕለት ተግባራችሁን አታከናውኑም፡፡ 36 የሚቃጠል መስዋዕት ታደርጋላችሁ፣ ለያህዌ ጣፋጭ መዓዛ ያለው መስዋዕት ታቀርባላችሁ፡፡ አንድ ወይፈን፣ አንድ አውራ በግ፣ እና ነውር ሌለባቸው ሰባት የአንድ አመት ወንድ ጠቦት በጎች ታቀርባላችሁ፡፡ 37 ለወይፈኑ፣ ለአውራ በጉ፣ እና ለጠቦቶቹ የእህል ቁርባናቸውንና የመጠጥ ቀርባናቸውን በተወሰነው ቁጥር መሰረት እንደ ትእዛዙ ታቀርባላችሁ፡፡ 38 ከመደበኛ የሚቃጠል መስዋዕት፣ አብሮት ከሚቀርበው የእህል ቁርባን፣ እና የመጠጥ ቁርባን በተጨማሪ ለኃጢአት መስዋዕት አንድ ወንድ ፍየል ማቅረብ አለባችሁ፡፡ 39 በተወሰነ ክብረ በዓላቶቻችሁ ለያህዌ የምታቀርቧቸው እነዚህ ናቸው፡፡ እነዚህም ከስለቶቻችሁና የበጎ ፈቃድ ስጦታዎቻችሁ በተጨማሪ የምታቀርቧቸው ናቸው፡፡ እነዚህን የሚቃጠሉ መስዋዕቶቻችሁ፣ የእህል ቁርባኖች፣ የመጠጥ ቁርባኖች፣ እና የህብረት መስዋዕቶች አድርጋችሁ አቅርቧቸው፡፡” 40 ሙሴ ያህዌ ለእስራኤል ሰዎች እንዲናገር ያዘዘውን ሁሉ ተናገረ፡፡



Numbers 29:1

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በሰባተኛውም ወር ከወሩ በመጀመሪያ ቀን

ይሄ የሚያመለክተው የዕብራውያንን ሰባተኛ ወር ነው፡፡“በ1ኛው ወር በ7ኛው ወር”(የዕብራውያን ወራትንናተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን ለማክበር የተቀደሰ ጉባዔ ይሁንላችሁ

“እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማክበር በአንድነት ተሰብሰቡ” “የተቀደሰ ጉባዔ”የሚለው ቃል ሰዎች እግዚአብሔርን ለማምለክ የሚሰበሰቡበት ሁኔታ ማለት ነው፡፡እግዚአብሔርን ማምለክ የተቀደሰ ክስተት ነው፡፡

እናንተ መለከቶችን የምትነፉበት ቀን ነው

“እናንተ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እዚህ ላይ የእሥራኤልን ሕዝብ የሚወክሉትን ካህናትን ነው፡፡ካህናት አምልኮው እንዲጀመር መለከትን ይነፋሉ ወይም ማህረሰቡ በአንድነት እንዲሰባሰብ ለማድረግ፡፡“ካህናት መለከቶችን የሚነፉበት ቀን ይሆናል”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:2

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

Numbers 29:3

የእህል ቁርባናቸውን

ይሄ የሚያመለክተው እያንዳንዱ እንስሳ በሚሰዋበት ወቅት አብረው መቅረብ የሚገባቸውን የእህል ቁርባኖችን ነው፡፡“ከአነርሱ ጋር አብረው የሚቀርቡት የእህል ቁርባኖች”ወይም “የሚያጅቧቸው የእህል ቁርባኖች”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

በዘይት የተለወሰ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሳችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ ሁለቱ ማለት ነው፡፡“አራት ተኩል ሊትር የሆነ መልካም ዱቄት”ወይም “ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን፤ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከመሥፈሪያው ሶስት አሥረኛ እጅ

“ሶስት አሥረኛ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች ሶስቱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ስድስት ሊትር”ወይም “የኢፍ መሥፈሪያ ሶስት አሥረኛ”(ስድስት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ አንድ እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ አንድ እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ አንዱ ማለት ነው፡፡“ሁለት ሊትር መልካም የሆነ ዱቄት”ወይም “አንድ አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

መሥዋዕትን ማቅረብ

“መሥዋዕት ማቅረብ”የሚለው ሐረግ “መሰዋት”በሚለው ሥም ሊገለፅ ይችላል፡፡(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:6

በሰባተኛው ወር..በወራቶቹ የመጀመሪያው ቀን

“በ7ኛ ወር…በእያንዳንዱ ወር በ1ኛው ቀን”“ወር”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የዕብራውያንን የወር አቆጠጠር ነው፡፡(የዕብራውያን ወራትንናተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

በየወሩ፤የተለየ የሚቃጠል መሥዋዕት …ከእርሱ ጋር

“በየወሩ፤የተለየ የሚቃጠል መሥዋዕት …ከእርሱ ጋር” ይሄ በየወሩ መጀመሪያ ላይ የሚደረግ መሥዋዕት ነው፡

በዘወትርም ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቁርባን፤ከመጠጡም ቁርባን

ይሄ የሚያመለክተው ካህናቱ በየዕለቱ መሥጠት የሚገባቸውን መሥዋዕት ነው፡፡የእህል ቁርባኑና የመጠጡቁርባን ዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር መቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡“ዘወትር የሚቀርበው የሚቃጠል መሥዋዕት አብረው ከሚቀርቡት ከእህል ቁርባንና ከመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

የተደነገገውን ትዕዛዝ ተግባራዊ ታደርጉታላችሁ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእግዚብሔርን ትዕዛዝ ተግባራዊ ታደርጉታላችሁ”ወይም “እግዚአብሔር ያዘዘውን ትዕዛዝ ተግባራዊ ታደርጉታላችሁ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር በእሣት የሚቀርብ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ በመሠዊያው ላይ ለእግዚአብሔር ያቃጠላችሁት ቁርባን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:7

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በሰባተኛው ወር..በወራቶቹ የመጀመሪያው ቀን

“በ7ኛ ወር…በእያንዳንዱ ወር በ1ኛው ቀን” “ወር”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የዕብራውያንን የወር አቆጠጠር ነው፡፡(የዕብራውያን ወራትንናተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን ለማክበር የተቀደሰ ጉባዔ ይሁንላችሁ

“እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማክበር በአንድነት ተሰብሰቡ” “የተቀደሰ ጉባዔ”የሚለው ቃል ሰዎች እግዚአብሔርን ለማምለክ የሚሰበሰቡበት ሁኔታ ማለት ነው፡፡እግዚአብሔርን ማምለክ የተቀደሰ ክስተት ነው፡፡

Numbers 29:9

በዘይት የተለወሰ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሳችሁት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከመሥፈሪያው ሶስት አሥረኛ እጅ

“ሶስት አሥረኛ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች ሶስቱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ስድስት ሊትር”ወይም “የኢፍ መሥፈሪያ ሶስት አሥረኛ”(ስድስት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ ሁለቱ ማለት ነው፡፡“አራት ተኩል ሊትር የሆነ መልካም ዱቄት”ወይም “ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን፤ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ አንድ እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ አንድ እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ አንዱ ማለት ነው፡፡“ሁለት ሊትር መልካም የሆነ ዱቄት”ወይም “አንድ አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

መሥዋዕትን ማቅረብ

“መሥዋዕት ማቅረብ”የሚለው ሐረግ “መሰዋት”በሚለው ሥም ሊገለፅ ይችላል፡፡(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:12

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በሰባተኛውም ወር..በአስራ አምስተኛው ቀን

“በ7ኛ ወር…በ15ኛው ቀን” “ወር”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የዕብራውያንን የወር አቆጠጠር ነው፡፡(የዕብራውያን ወራትንናተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርን ለማክበር የተቀደሰ ጉባዔ ይሁንላችሁ

“እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማክበር በአንድነት ተሰብሰቡ” “የተቀደሰ ጉባዔ”የሚለው ቃል ሰዎች እግዚአብሔርን ለማምለክ የሚሰበሰቡበት ሥርዓት ማለት ነው፡፡እግዚአብሔርን ማምለክ የተቀደሰ ሁኔታ ነው፡፡

በዓሉን ለእርሱ ልትጠብቁት ይገባል

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“መጠበቅ”የሚለው ቃል መከታተል ወይም ማክበር ማለት ነው፡፡“እርሱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ነው፡፡“በዓሉን ለእግዚአብሔር መጠበቅ ይኖርባችኋል”ወይም “በዐሉን ለእግዚአብሔር ልታከብሩት ይገባል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በእሳት የሚደረግ መሥዋዕት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በመሠዊያ ላይ ልታቃጥሉት ይገባል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አራት ወይፈኖች፤ሁለት አውራ በጎች፤አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት ጠቦቶች

“14 ወይፈኖች፤2 አውራ በጎች፤14 የአንድ ዓመት ተባት ጠቦቶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:14

በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዘይት የለወሳችሁት መልካም ዱቄት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከመሥፈሪያው ሶስት አሥረኛ እጅ

“ሶስት አሥረኛ”ማለት አሥር እኩል ከሆኑ ክፍሎች ሶስቱ ማለት ነው፡፡ይሄ ዘመናዊ በሆነ መለኪያ ሊፃፍ ይችላል፡፡“ስድስት ሊትር”ወይም “የኢፍ መሥፈሪያ ሶስት አሥረኛ”(ስድስት ሊትር ያህል ይሆናል)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ ሁለት እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ ሁለት እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ ሁለቱ ማለት ነው፡፡“አራት ተኩል ሊትር የሆነ መልካም ዱቄት”ወይም “ሁለት አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን፤ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሥር እጅ አንድ እጅ

“የኢፍ መሥፈሪያ መልካም ዱቄት”የሚለው ቃል በበፊቱ ሐረግ ግልፅ ተደርጓል፡፡ይሄ ሊደገምም ይችላል፡፡“ከአሥር እጅ አንድ እጅ”ማለት እኩል ከሆኑ አሥር ክፍሎች ውስጥ አንዱ ማለት ነው፡፡“ሁለት ሊትር መልካም የሆነ ዱቄት”ወይም “አንድ አሥረኛ የኢፍ መሥፈሪያ”(4.5 ያህል የሚሆን)(ክፍልፋዮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ሚዛን የሚለውን ይመልከቱ)

መሥዋዕትን ማቅረብ

“መሥዋዕት ማቅረብ”የሚለው ሐረግ “መሰዋት”በሚለው ሥም ሊገለፅ ይችላል፡፡(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባኑና የመጠጥ ቁርባኑ ዘወትር ከሚቀርበው የሚቃጠል መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡

Numbers 29:17

በጉባዔው በሁለተኛው ቀን

“በበዓሉ 2ተኛ ቀን” እዚህ ላይ “ጉባዔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በበዓሉ ወቅት ያሉትን ሣምንታት ነው፡፡(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አራት ወይፈኖች፤ሁለት አውራ በጎች፤አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት ጠቦቶች

“14 ወይፈኖች፤2 አውራ በጎች፤14 የአንድ ዓመት ተባት ጠቦቶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በታዘዙት መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:20

በጉባዔው በሶስተኛው ቀን

“በበዓሉ 3ተኛ ቀን” እዚህ ላይ “ጉባዔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በበዓሉ ወቅት ያሉትን ሣምንታት ነው፡፡(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አንድ ወይፈኖች፤ሁለት አውራ በጎች፤አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት ጠቦቶች

“11 ወይፈኖች፤2 አውራ በጎች፤14 የአንድ ዓመት ተባት ጠቦቶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በታዘዙት መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:23

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በጉባዔው በአራተኛው ቀን

“በበዓሉ 4ተኛ ቀን” እዚህ ላይ “ጉባዔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በበዓሉ ወቅት ያሉትን ሣምንታት ነው፡፡(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አራት ተባት ጠቦቶች

“14 ተባት ጠቦቶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በታዘዙት መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:26

በጉባዔው በአምስተኛው ቀን

“በበዓሉ 5ተኛ ቀን” እዚህ ላይ “ጉባዔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በበዓሉ ወቅት ያሉትን ሣምንታት ነው፡፡(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አራት ተባት ጠቦቶች

“14 ተባት ጠቦቶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በታዘዙት መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:29

በጉባዔው በስድስተኛው ቀን

“በበዓሉ 6ተኛ ቀን” እዚህ ላይ “ጉባዔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በበዓሉ ወቅት ያሉትን ሣምንታት ነው፡፡(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አራት ተባት ጠቦቶች

“14 ተባት ጠቦቶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በታዘዙት መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:32

በጉባዔው በሰባተኛው ቀን

“በበዓሉ 7ተኛ ቀን” እዚህ ላይ “ጉባዔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በበዓሉ ወቅት ያሉትን ሣምንታት ነው፡፡(ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ አራት ተባት ጠቦቶች

“14 ተባት ጠቦቶች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በትዕዛዙ መሠረት

“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:35

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሕዝቡ ማድረግ ያለበትን ነገር እግዚአብሔር መንገሩን እንደቀጠለ ነው፡፡

በስምንተኛውም ቀን

“ስምንተኛው”የሚለው ቃል ስምንት ለሚለው ተከታታይ ቁጥር ነው፡፡ (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ሌላ የተቀደሰ ጉባዔ ይሁንላችሁ

“እግዚአብሔርን ለማምለክ እንደገና ተሰብሰቡ”ይሄ ከመጀመሪው ቀን በዓል ጋር የሚመሳሰል ሌላ ጉባዔ ነው፡፡

በእሣት የሚደረግ መሥዋዕት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በመሠዊያው ላይ ማቃጠል ይኖርባችኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:37

የእህል ቁርባናቸውና የመጠጥ ቁርባናቸው

እነዚህ መሥዋዕቶች መቅረብ የሚኖርባቸው ከወይፈን፤ከበግ ጠቦትና ከአውራ በግ ጋር ነበር፡፡”የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

በታዘዙት መሠረት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእህሉ ቁርባንና ከመጠጡ ቁርባን

የእህሉ ቁርባን ከሚቃጠለው ቁርባን ጋር መቅረብ ነበረበት፡፡የመጠጥ ቁርባኑ ከኃጢአት መሥዋዕቱና ከሚቃጠለው መሥዋዕቱ ጋር አብሮ መቅረብ ነበረበት፡፡“አብረው ከሚቀርቡት የእህል ቁርባንና የመጠጥ ቁርባን ጋር”(ንብረት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 29:39

የምታቀርቧቸው ነገሮች እነዚህ ናቸው

“የምታቀርቧቸው መሥዋዕቶች እነዚህ ናቸው”

በተቆረጠላቸው ቀን የሚደረጉ በዓላት

“በዕቅድ የተያዙ በዓላት”እነዚህ በዓላት በተያዘላቸው የጊዜ ሠሌዳ መሠረት በቋሚነት የሚከናወኑ ናቸው፡፡“በተቆረጠላቸው”ማለት“በተመደበላቸው”ወይም“አስቀድሞ በተወሰነላቸው”ጊዜ ማለት ነው፡፡


Chapter 30

1 ሙሴ ለእስራኤል ህዝብ የጎሳ መሪዎች እንዲህ አላቸው፣ “ያህዌ ያዘዘው ይህን ነው፡፡ 2 ማንም ሰው ለያህዌ ስዕለት ሲሳል፣ ወይም በቃል ኪዳን ራሱን በመሀላ ሲያስር፣ ቃሉን ማፍረስ የለበትም፡፡ ከአፉ የወጣውን ማናቸውንም ነገር ለማድረግ ቃልኪዳኑን መጠበቅ አለበት፡፡ 3 አንዲት ወጣት ሴት በአባቷ ቤት እያለች ለያህዌ ብትሳልና በመሀላ ራሷን ብታስር፣ 4 አባቷም ስዕለቷንና ራሷን ያሰረችበትን መሀላ ቢሰማ፣ እርሱም እርሷን ለመመለስ አንዳች ነገር ባይናገር መሀላዎቿ ሁሉ መፈፀም አለባቸው፡፡ ራሷን ያሰረችባቸው ቃልኪዳኖች ሁሉ ተግባራዊ ይሆናሉ፡፡ 5 ነገር ግን አባቷ ስለ ስዕለቷና ስለገባችው ቃል ኪዳን ሰምቶ ምንም ነገር ባይነግራት በራሷ ላይ የወሰደቻቸው የገባቻቸው መሀላዎችና ቃል ኪዳኖች መፈጸም አለባቸው፡፡ 6 ሆኖም ግን፣ አባቷ የገባቻቸውን መሀላዎች ሁሉና የከበሩ ቃል ኪዳኖቿን ራሷን ግዴታ ውስጥ ያስገባችበትን ነገር ቢሰማ፣ ደግሞም በዚያው ቀን ማድረግ ያለበትን ቢነግራት መሀላዋን ለመፈጸም አትገደድም፡፡ ያህዌ ይቅር ይላታል ምክንያቱም አባቷ ማድረግ ያለባትን ነግሯታል፡፡ 7 እነዚያ መሀላዎች እያሉባት ባል ብታገባ ወይም በችኮላ መሀላ ብታደርግና ራሷን ግዴታ ውስጥ ብታስገባ እነዚያ ግዴታዎች መፈጸም አለባቸው፡፡ 8 ነገር ግን ባሏ በዚያው ቀን ሰምቶ ቢከለክላት የገባቸውን መሀላና በችኮላ ራሷን ያሰረችበትን መሀላዋን ያስቀራል፡፡ ያህዌ ከዚህ ነጻ ያደርጋታል፡፡ 9 ባሏ የሞተባት ወይም ከባሏ የተፋታች ሴት ግን ራሷን የሰራችባቸው ነገሮች ሁሉ ተፈፃሚ ይሆኑባታል፡፡ 10 ከባሏ ቤተሰቦች ጋር ያለች ሴት ብትሳል ራሷን በቃል ኪዳን መሀላ ብታስር፣ 11 እና ባልዋ ሰምቶ ምንም ነገር ባይነግራት ስእለቷን ባያስቀር፣ ስዕለቶቿ ሁሉ መፈጸም አለባቸው፡፡ ራሷን ያሰረችባቸው ቃልኪዳኖች ሁሉ መፈጸም አለባቸው፡፡ 12 ነገር ግን ባሏ ስለ ስዕለቶቿ በሰማ ቀን እንዲቀሩ ካደረገ፣ ስለ ስዕለቶቿ ወይም ቃልኪዳኖቿ ከከንፈሯ የወጡ ነገሮች ሁሉ የግዴታ መፈጸም አይኖርባቸውም፡፡ ባልዋ አስቀርቷቸዋል፡፡ ያህዌ ነጻ ያደርጋታል፡፤ 13 አንዲት ሴት የገባችውን እያንዳንዱን መሀላ ወይም ስእለት እንድታጥፍ የሚያደርጋትን አንዳች ነገር በባሏ ሊጸና ወይም ሊሻር ይችላል፡፡ 14 ነገር ግን ቀናት ሲያልፉ ባሏ አንዳች ካልነገራት፣ ስዕቶቿን ሁሉ እና ቃል የገባቻቸውን ነገሮች ያፀናባታል፡፡ ስዕቶቿንና መሀላዎቿን የሚያፀናባት ስለእነዚህ በሰማበት ጊዜ ምንም ስላልነገራት ነው፡፡ 15 ባሏ የሚስቱን ስዕለት ከሰማ ከረጅም ጊዜ በኋላ ሊሽር ቢሞክር፣ ስለእርሷ ኃጢአት ሀላፊነቱን ይወስዳል፡፡” 16 ያህዌ ሙሴ እንዲያውጃቸው የሰጠው ቋሚ መመሪያዎች እነዚህ ናቸው፡፡ በአንድ ወንድና በሚስቱ መሀል፣ እንዲሁም በአባትና በወጣትነቷ በአባቷ ቤት ስለምትኖር ሴት ልጁ ያህዌ የሰጠው ቋሚ መመሪያ ይህ ነው፡፡



Numbers 30:1

ሰው ለእግዚአብሔር ስእለት ቢሳል ወይም ራሱ በመሐላ ቢያስር

እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን በጋራ እንዲቀርቡ የተደረጉት ስለ ስእለትና ስለ መሐላ አፅንኦት ለመስጠት ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ራሱ በመሐላ ቢያስር

ሙሴ እዚህ ላይ የሚናገረው አንድ ሰው አንድ ነገር ለማድረግ ቃል የመግባቱን ጉዳይ አስመልክቶ ቢሆንም የሚገባው ቃል ቁሣቁስ ይመስል ራሱ ላይ እንደሚያስረው ዓይነት አድርጎ ያቀርበዋል፡፡“አንድ ነገር ለመፈፀም ራስን መሥጠት”ወይም “አንድን ነገር ለመፈፀም ቃል መግባት” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ቃሉን አይስበር፤ከአፉ እንደወጣው ሁሉ ያድርግ

እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን በጋራ እንዲቀርቡ የተደረጉት የገባውን ቃል ተግባራዊ ማድረግ እንደሚኖርበት አፅንኦት ለመስጠት ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ቃሉን አይስበር

“ቃሉን”የሚለው ቃል የሚያመለክተው የሰውዬውን መሐላና ቃል ኪዳን መግባት ነው፡፡ሙሴ እነዚሀን ነገሮች ተግባራዊ አለማድረግን ልክ አንድን ዕቃ ከመስበር ጋር አመሳስሎ ነው የሚናገረው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ከአፉ እንደወጣው ሁሉ

እዚህ ላይ“አፍ”የሚለው ቃል ሰውዬው የሚናገረውን ነገር ለመግለፅ የዋለ ነው፡፡“አደርገዋለሁ የሚለውን ነገር ሁሉ ማድረግ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 30:3

ራሷን በስእለት ብታስር

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የመግባቷን ጉዳይ ልክ ራሷን በአንድነገር እንደምታስረው ዓይነት አድርጎ ነው ያቀረበው፡፡“የገባቸውን ቃል ለመፈፀም ራሷን ሰጠች”ወይም “አንድ ነገር ለመፈፀም ቃል ገባች”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

መሐላውና ቃል መግባቱ

እነዚህ ሁለቱ ሐረጎች ተመሳሳይ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡አፅንኦት የሚሰጠው የገባችውን ቃል በሚመለከት ነው፡፡“መሐላው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ራሷን ባሰረችበት

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የገባቸውን ነገር ለመፈፀም ስትል የምታደርገውን መሠጠት ልክ ከሰውነቷጋር እንዳሰረችው ቁሣቁስ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡“የገባቸውን ቃል ለመፈፀም ራሷን ሰጠች”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ብታጥፍ

“ያለችውን ነገር ብትሰረዘው”

ስእለትዋ ሁሉ ይፀናል..መሐላ ሁሉ ይፀናል

እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ያላቸው ሲሆን መሐላዋን ሁሉ መጠበቅ እንዳለባት አፅነዖት የሚሰጥ ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

ይፀናል

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን መሐላዋ የፀና እንደሆነና ተግባራዊ ማድረግ እንደሚጠበቅባት የሚያስረዳ ነው፡፡“ተግባራዊ እንድታደርገው ትገደዳለች”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 30:5

መሐላዋና ቃል መግባቷ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች በጣም የተመሳሰለ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡ቃል የገባቸውን ነገር አጥብቀው የሚያሳስቡ ናቸው፡፡“መሐላዋን”(ሁለት ተመሳሳይ የሆነ ገፅታ ያላቸው የሚለውን ይመልክቱ)

ራስዋ ላይ ያደረገችው

እዚህ ላይ ሴትዬዋ መሐላዋን ለመፈፀም ራሷን መሥጠቷን ልክ መሐላውን ሰውነቷ ላይ እንደምታደርገው ልብስ ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ራሷን የሰጠችበት”ወይም “ቃል የገባችው”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ይፀናል

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን መሐላዋ የፀና እንደሆነና ተግባራዊ ማድረግ እንደሚጠበቅባት የሚያስረዳ ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 30፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ተግባራዊ እንድታደርገው ትገደዳለች”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 30:6

በተረጋጋ መንፈስ ውስጥ ሆና ራስዋን ያሰረችበት መሐላ

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የገባቸውን ነገር ለመፈፀም ስትል የምታደርገውን መሠጠት ልክ ከሰውነቷጋር እንዳሰረችው ቁሣቁስ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡“ ረጋ ባለ መንፈስ ቃል የገባችውን ነገር ለመፈፀም የምታደርገው መሠጠት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ዝም ቢላት

እዚህ ላይ የሴትዋን ቃል ዝም ማለቱን ልክ አንድ ባለሥልጣን በሥልጣኑ እንደሚከለክላት ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የፀና አይሆንም

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን መሐላዋ የፀና እንደማይሆንና ተግባራዊ ማድረግ እንደማይጠበቅባት የሚያስረዳ ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 30፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ተግባራዊ እንድታደርገው አትገደድ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔርም ይቅር ይላታል

ይሄ የሚያመለክተው መሐላዋን ባትፈፀምም እንኳን እግዚአብሔር ይቅር ያላት መሆኑን ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“መሐላዋን ባትፈፅምም እግዚአብሔር ይቅር ይላታል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእነዚያ መሐላዎች ሥር ከሆነ

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡መሐላዋ የፀና እንደማይሆንና ተግባራዊ ማድረግ እንደማይጠበቅባት የሚያስረዳ ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 30፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ተግባራዊ እንድታደርገው አትገደድ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በችኮላ

በአግባቡ ሳይታሰብ የሚደረግ ነገር፡፡

እነዚያ ግዴታዎች

“ግዴታዎች”የሚለው ቃል “ማስገደድ”በሚለው ሥም ሊገለፅ ይችላል፡፡“ራስዋን ግዴታዎች ውስጥ ያስገባችባቸው ነገሮች”(አሕፅሮተ ሥም የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 30:8

ያደረገችው መሐላ…በችኮላ የተናገረችው ንግግር

“ያደረገችው መሐላ…ማለትም በችኮላ የተናገረችው ንግግር” እነዚህ ሁለት ዓረፍተ ነገሮች የሚያመለክቱት አንድን ነገር ነው፡፡ሁለተኛው ሐረግ ሴትዬዋ ያደረገችውን መሐላ የሚገልፅ ነው፡፡(ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

የአንደበቷ ችኩል አነጋገር

“ችኩል አነጋገር”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በችኮላ የገባችውን የተስፋ ቃል ነው፡፡እዚህ ላይ “አንደበቷ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ራሷን ሴትዬዋን ነው፡፡አንደበቷ ከምትናገረው ነገር ጋር የተያያዘ በመሆኑ “አንደበቷ”በሚለው ቃል ተወክላለች፡፡“በችኮላ የተናገረቻቸው ነገሮች” ወይም“በችኮላ ቃል መግባቷ”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

ራስዋን ያሰረችበትን

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የገባቸውን ነገር ለመፈፀም ስትል የምታደርገውን መሠጠት ልክ ከሰውነቷ ጋር እንዳሰረችው ቁሣቁስ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡“ ረጋ ባለ መንፈስ ቃል የገባችውን ነገር ለመፈፀም የምታደርገው መሠጠት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ነፃ ያወጣታል

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የገባችውን ነገር ባትፈፅምም እግዚአብሔር ይቅር እንደሚላት ለመግለፅ ከታሰረችበት ነገር እንደምትለቀቅ ዓይነት አድርጎ አቅርቦታል፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ይቅር ይላታል” “የገባችውን ቃል ባትፈፅምም እግዚአብሔር ይቅር ይላታል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ))

Numbers 30:9

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እግዚአብሔር ያዘዘውን ነገር ለነገድ መሪዎች መናገሩን ይቀጥላል፡፡

የተፋታች ሴት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንድ ሰው የፈታት ሴት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ራስዋን ያሰረችበትን

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የገባቸውን ነገር ለመፈፀም ስትል የምታደርገውን መሠጠት ልክ ከሰውነቷ ጋር እንዳሰረችው ቁሣቁስ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡“ቃል የገባችውን ነገር ለመፈፀም የምታደርገው መሠጠት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በእርሷ ላይ የፀና ይሆናል

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን መሐላዋ የፀና እንደሆነና ተግባራዊ ማድረግ እንደሚጠበቅባት የሚያስረዳ ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 30፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ተግባራዊ እንድታደርገው ትገደዳለች”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሴት በባሏ ቤት ውስጥ ሳለች ብትሳል

ይሄ የሚመለከተው ያገቡ ሴቶችን ነው፡፡የዚሀን ሃሣብ የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡“ያገባች ሴት ስእለት ብትሳል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ከዚያ በኋላ መሐላዋ ሁሉ የፀና ይሆናል…መተግበሩ ግዴታ ይሆናል

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡“መተግበሩ ግዴታ ይሆናል”የሚለው ቃል የሚፀናና እርሱን ለመፈፀም ትገደዳለች ማለት ነውየዚህን ተመሳሳይ ሐረግ በኦሪት ዘኁልቁ 30፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ከዚያም መሐላዋን ሁሉ ተግበራዊ ማድረግ ይኖርባታል….መፈፀም ይኖርባታል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ስእለትዋ ይፀናል…ራስዋንም ያሰረችበት መሐላ ሁሉ ይፀናል

በመሠረቱ እነዚሀ ዓረፍተ ነገሮች ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆን ተደጋገመው የቀረቡት ለጉዳዩ አፅንዖት ለመሥጠት ሲሆን ተቀናጀተውም ሊቀርቡ ይችላሉ፡፡“ስእለቷና መሐላዋ ሁሉ የፀና መሆን ይኖርበታል” (ተመሳሳይነት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 30:12

ከከንፈሯ የወጣ ማንኛውም ነገር

እዚህ ላይ ሴትዬዋ የተናገረችው ንግግር ከከንፈሯ እንደወጣ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ከዚያ በኋላ የተናገረችው ነገር ሁሉ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

የፀና አይሆንም

ይሄ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን መሐላዋ የፀና እንደማይሆንና ተግባራዊ ማድረግ እንደማይጠበቅባት የሚያስረዳ ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 30፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“ተግባራዊ እንድታደርገው አትገደድ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር ነፃ ያወጣታል

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የገባችውን ነገር ባትፈፅምም እግዚአብሔር ይቅር እንደሚላት ለመግለፅ ከታሰረችበት ነገር እንደምትለቀቅ ዓይነት አድርጎ አቅርቦታል፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ይቅር ይላታል” “የገባችውን ቃል ባትፈፅምም እግዚአብሔር ይቅር ይላታል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውንና (በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ))

Numbers 30:13

ስእለትዋን ሁሉ …መሐላዋን ሁሉ በልዋ ያጸናዋል፤ባልዋም ከንቱ ያደርገዋል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የአንዲት ሴት ባል ራሰዋን ያሰረችበትን ማንኛውንም ነገር ማለትም ስእለት ወይም መሐላ ማጽናት ወይም ማፍረስ የሚችልበት ሁኔታ ይኖራል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የታሰረችበትን

እዚህ ላይ ሙሴ አንዲት ሴት ቃል የገባችውን ነገር ለመፈፀም ስትል የምታደርገውን መሠጠት ልክ ከሰውነቷ ጋር እንዳሰረችው ቁሣቁስ አድርጎ ነው የሚያቀርበው፡፡“ቃል የገባችውን ነገር ለመፈፀም የምታደርገው መሠጠት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አሳሪ የሆኑ ቃል ኪዳኖች

ሙሴ አንዲት ሴት የምትገባቸው ቃል ኪዳኖች አካሏን እንደሚያስሩ ነገሮች አድርጎ አቅርቧቸዋል፡፡“ግዴታዎች” “ቃል ኪዳኖች”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ዝም በሏታልና

ግልፅ የሆነውን ይህንን መረጃ የበለጠ ልታብራሩት ትችላላችሁ፡፡“ጉዳዮቹን አስመልክቶ ምንም ነገር ስላልተናገረ”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 30:15

ስለ ኃጢአቷ ኃላፊነቱን እርሱ የሚወስድ ይሆናል

ስእለቷን የማትፈፀም ከሆነ በእርሷ ምትክ ኃጢአቷን ይሸከማል ማለት ነው፡፡የዚህ ዓረፍተ ነገር ሙሉ ሃሣብ የበለጠ ሊብራራ ይችላል፡፡“ስእለቷን ባትፈፀም በኃጢአቷ ጥፋተኛ አትባልም፡፡እርሱ ግን በእርሷ ምትክ ጥፋተኛ የሚሆን ይሆናል፡፡”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 31

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “የእስራኤል ህዝብ ምድያማውያንን ይበቀሉ፡፡ ያን ካደረግህ በኋላ፣ ወደ ወገኖችህ ትከማቻለህ፡፡” 3 ስለዚህም ሙሴ ለህዝቡ እንዲህ አለ፣ “በምድያማውያን ላይ የያህዌን በቀል ይፈጽሙ ዘንድ ከወንዶቻችሁ አንዳንዶቹን ወደ ጦርነት እንዲወጡ አስታጥቋቸው፡፡ 4 እያንዳንዱ በእስራኤል ውስጥ ያለ ጎሳ ለጦርነት አንድ ሺህ ወታደሮችን መላክ አለበት፡፡” 5 ስለዚህ ከእስራኤል ብዙ ሺህ ወንዶች መሀል ከእያንዳንዱ ጎሳ አንድ ሺህ ሰው ለጦርነት ቀረበ፣ በጠቅላላው አስራ ሁለት ሺህ ወንዶች ነበሩ፡፡ 6 ከዚያ ሙሴ ከየጎሳው አንድ ሺህ ሰዎችን ከካህኑ ከአልዓዛር ልጅ ከፊንሃስ ጋር እና ከተቀደሰው ስፍራ ከጥቂት ቁሳቁሶችና እንዲሁም ምልክቶችን ለማሰማት በእጁ ያሉትን መለከቶች አስይዞ ወደ ጦርነት ላካቸው፡፡ 7 እነርሱም ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው ከምድያማውያን ጋር ተዋጉ፡፡ ሰዎቹን ሁሉ ፈጇቸው፡፡ 8 የምድያምን ነገስታት ኤዊ፣ ሮቆም፣ ሱር ሑርን እና እና ሪባን ከተቀሩት ጋር በሰይፍ ገደሏቸው፡፡ 9 የእስራኤል ጦር፤ የምድያምን ሴቶች፣ ልጆቻቸውን ከብቶቻቸውን ሁሉ፣ መንጋዎቻቸውን እና ንብረቶቻቸውን ሁሉ ምርኮ አደረጉ፡፡ እዚህን ሁሉ ዘርፈው ወሰዱ፡፡ 10 የሚኖሩባቸውን ከተሞችና ሰፈሮች ሁሉ አቃጠሉ፡፡ 11 የሰውና እንስሳት ምርኮዎቻቸውንና እስረኞችን ወሰዱ፡፡ 12 እስረኞችን፣ የዘረፉትን፣ እና የያዙትን ነገሮች ወደ ሙሴ፣ ወደ ካህኑ አልዓዛር፣ እና ወደ እስራኤል ማህበረሰብ አመጡ፡፡ እነርሱም እነዚህን ኢያሪኮ አጠገብ ዮርዳስ፣ በሞአብ ሜዳ ላይ ወደ ሚገኘው ሰፈር አመጡ፡፡ 13 ሙሴ፣ ካህኑ አልዓዛር፣ እና የማህበረሰቡ መሪዎች በሙሉ ሊቀበሏቸው ከሰፈር ወጡ፡፡ 14 ሙሴ ግን ከጦርነት በተመለሱት በጦሩ መኮንኖች፣ በሻለቃዎችና በመቶ አለቆች ላይ ተቆጥቶ ነበር፡፡ 15 ሙሴ መኮንኖቹን እንዲህ አላቸው፣ “ሴቶቹ ሁሉ በህይወት እንዲኖሩ ተዋችኋቸውን?” 16 እነዚህ ሴቶች በበለዓም ምክር፣ የእስራኤል ህዝብ በያህዌ ላይ በፌጎር ኃጢአት እንዲሰራና መቅሰፍት እንዲወርድበት ያደረጉ ናቸው፡፡ 17 ስለዚህ አሁን፣ ትናንሾቹን ወንዶች ሁሉ ግደሉ፣ ከወንድ ጋር የተኙ ሴቶችን ሁሉ ግደሉ፡፡ 18 ከወንድ ጋር ተኝተው የማያውቁትን ወጣት ልጃገረዶች ግን ለራሳችሁ ውሰዱ፡፡ 19 ከእስራኤል ሰፈር ውጭ ለሰባት ቀናት መቆየት አለባችሁ፡፡ ማንንም ሰው የገደላችሁ ሁሉና ወይም የሞተ ሰው የነካችሁ ሁሉ በሶስተኛው ቀንና በሰባተናው ቀን ራሳችሁን ማንጻት አለባችሁ፡፡ እናንተና ምርኮኞቻችሁ መንጻት አለባችሁ፡፡ 20 ልብሶቻችሁን አንጹ፣ ከእንስሳት ቆዳ እና ከፍየል ፀጉር የተሰሩ ማናቸውንም ነገሮች፣ እንዲሁም ከእንጨት የተሰሩ ነገሮችን ሁሉ አንጹ፡፡” 21 ካህኑ አልዓዛር ወደ ጦርነት የሄዱትን ወታደሮች እንዲህ አላቸው፣ “ይህ ያህዌ ለሙሴ የሰጠው የተደገነገገ ህግ ነው፡ 22 ወርቁ፣ ብሩ፣ ነሀሱ፣ ብረቱ፣ ቆርቆሮውና እርሳሱ 23 እና ማናቸውም እሳት የሚቋቋምን ነገር በእሳት ውስጥ አሳልፉት እናም የተቀደሰ ይሆናል፡፡ እነዚያን ነገሮች በማንጻት ውሃ አንጹዋቸው፡፡ በእሳት ውስጥ ማለፍ የማይችለውን ማናቸውንም ነገር በውሃ አንጹ፡፡ 24 እናም ልብሶችሁን በሰባተኛው ቀን እጠቡ፣ ከዚያም የተቀደሳችሁ ትሆናላች፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ እስራኤል ሰፈር መግባት ትችላላችሁ፡፡” 25 ከዚያም ያህዌ ሙሴን እንደዚህ አለው፣ 26 ”ሰዎችም ይሁኑ እንስሳት፣ የተማረኩትንና የተወሰዱትን ነገሮች ሁሉ ቁጠሩ፡፡ አንተ፣ ካህኑ አልዓዛር፣ እና የማህበረሰቡ መሪዎች እንዲሁም የጎሳ አባቶች 27 ምርኮዎቹን ለሁለት ክፍል ክፈሏቸው፡፡ ለጦርነት በወጡ ወታደሮችና በተቀረው ማህበረሰብ መሃል ምርኮውን አከፋፍሉ፡፡ 28 ከዚያ ወደ ጦርነት ከወጡ ወታደሮች ለእኔ የሚሰጥ ግብር ጣል፡፡ ይህ ግብር ከሰዎችም ይሁን፣ ከቀንድ ከብት፣ ከአህዮች፣ ከበጎች ወይም ከፍየሎች ከየአምስት መቶው አንዱ ይሁን፡፡ 29 ይህን ግብር የእነርሱ ከሆነው ከከፊሉ ድርሻቸው ወስደህ ለእኔ የሚቀርብ ስጦታ እንዲሆን ለካህኑ አልዓዛር ስጠው፡፡ 30 ደግሞም ከከፊሉ የእስራኤል ህዝብ ድርሻ ከሆነው ሰዎች፣ ከቀንድ ከብቶች፣ ከአህዮች፣ ከበጎች ከፍየሎች፣ ከየሀምሳው መሀል አንዱን ወሰድ፡፡ እነዚህን ማደሪያዬን ለሚያገለግሉት ለሌዋውያን ስጣቸው፡፡” 31 ስለዚህ ሙሴና ካህኑ አልዓዛር ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው አደረጉ፡፡ 32 ወታደሮቹ በዝብዘው የወሰዱት ምርኮ 675000 በጎች፣ 33 ሰባሁለት ሺህ በሬዎች፣ 34 ስልሳ አንድ ሺህ አህዮች፣ 35 እና ሰላሳ ሁለት ሺህ ከወንድ ጋር ያልተኙ ሴቶች ነበሩ፡፡ 36 ለወታደሮች የተጠበቀላቸው ግማሹ 337000 በጎች ነበሩ፡፡ 37 ከዚህ ውስጥ የያህዌ ድርሻ 675 በጎች ነበር፡፡ 38 በሬዎቹ ሰላሳ ስድስት ሺህ ሲሆኑ የያህዌ ግብር 72 ነበር፡፡ 39 አህዮች 30500 ነበሩ፣ ከዚህ ውስጥ የያህዌ ድርሻ 61 ነበር፡፡ 40 ሰዎቹ አስራ ስድስት ሺ ሴቶች ነበሩ፣ ከዚህ ውስጥ ለያህዌ የተሰጠው ግብር 32 ነበር፡፡ 41 ሙሴ ለያህዌ የሚቀርቡትን ስጦታዎች ግብር ወሰደ፡፡ እርሱም ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው ለካህኑ አልዓዛር ይህንን ሰጠ፡፡ 42 ሙሴ ወደ ጦርት ከሄዱ ወታደሮች የወሰደውን የእስራኤል የሆነውን ግማሽ ምርኮ በተመለከተ፤ 43 የማህበረሰቡ ከምርኮ ግማሹ 337500 በጎች፣ 44 ሰላሳ ስድስት ሺህ በሬዎች፣ 45 ሰላሳ ሺ አምስት መቶ አህዮች፣ 46 እና አስራ ስድስት ሺ ሴቶች ነበሩ፡፡ 47 ከእስራኤል ህዝብ ግማሽ ከሆነ ድርሻው፣ ሙሴ ከሰውም ሆነ ከእንስሳት ከየአምሳው መሀል አንድ ወሰደ፡፡ እርሱም ያህዌ እንዲያደርገው ባዘዘው መሠረት የያህዌን ማደሪያ ለሚያገለግሉ ለሌዋውያን እነዚህን ሰጠ፡፡ 48 ከዚያ የሰራዊቱ መኮንኖች፣ የሻለቃ አዛዦች እና የመቶ አለቆች ወደ ሙሴ መጡ፡፡ 49 እንዲህም አሉ፣ “ባሮችህ በእኛ ስር ያሉትን ወታደሮች ቆጠርን፣ አንድ ሰው እንኳን አልጎደለም፡፡ 50 እኛ የያህዌን ስጦታ አምጥተናል፣ እያንዳንዱ ሰው ያገኘውን፣ የወርቅ ዕቃዎች፣ አልቦዎችና አንባሮች፣ የጣት ቀለበቶች፣ የጆሮ ጉትቻዎች፣ እና የአንገት ሀብሎች ማስተስረያ እንደሆነን በያህዌ ፊት አምጥተናል፡፡” 51 ሙሴና ካህኑ አልዓዛር ወርቁንና የእጁ ጥበብ ውጤት የሆኑትን የጌጥ ዕቃዎች ሁሉ ከእነርሱ ተቀበሉ፡፡ 52 ለያህዌ ያቀረቧቸው የወርቅ ስጦታዎች ሁሉ ከሻለቃዎችና ከመቶ አለቃዎች የተቀበሏቸው ስጦታዎች ክብደታቸው 16750 ሰቅሎቸ ነበር፡፡ 53 እያንዳንዱ ወታደርና እያንዳንዱ ሰው ከምርኮው ለራሱ ወስዷል፡፡ 54 ሙሴና ካህኑ አልዓዛር ከሻለቆችና ከመቶ አለቆች ወርቁን ወሰዱ፡፡ ለያህዌ የእስራኤል ህዝብ ማስታወሻ አድርገው ወርቁን ወደ መገናኛው ድንኳን አስገቡት፡፡



Numbers 31:1

ስለ እሥራኤል ልጆች በቀል ምድያማውያንን ተበቀል

ምድያማውያን እሥራኤላውያን ጣኦት እንዲያመልኩ በመገፋፋታቸው ምክኒያት እግዚአብሔር ሊቀጣቸው ነው፡፡

ከዚያም በኋላ ትሞታለህ ወደ ወገኖችህም ትከማቻለህ

በመሠረቱ እነዚህ ሐረጎች ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም ነው ያላቸው፡፡ይሄ ጨዋ በሆነ አነገገር ቡሴ የመሞቻው ጊዜ መሆኑንና መንፈሱ አባቶቹ ወዳሉበት የሚሄድ መሆኑን የሚገልፅ ነው፡፡ (ተመሳሳይነት የሚለውንና ሥርዓት የሌለውን አነጋገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:3

ከእናንተ መካከል ሰዎች ለጦርነት ይሰለፉ፡፡

“ከሰዎችህ መካከል ለተወሰኑት ሰዎች መሣሪያ አስታጥቃቸው”

ስለ እግዚአብሔር በቀል ምድያማውያንን ይበቀሉ

“ሄደህ ከምድያማውያን ጋር በመዋጋት ላደረጉት ነገር ቅጣትን ሥጣቸው”

አንድ ሺህ…ሁለት ሺህ

“1000…2000”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል አንድ ሺህ ሰዎች

“ከእሥራኤል አንድ ሺህ ወንዶች”

ከየነገዱ አንድ ሺህ ሰው ለጦርነት የሚሰለፉ ሰዎችተሰጡ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ከእያንዳንዱ ነገድ 1000 ሰዎች ለጦርነት ተላኩ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ ሁለት ሺህ ለጦርነት የተዘጋጁ ሰዎች

የሌዊን ነገድ ጨምሮ 12ቱም ነገዶች ሰዎችን ላኩ፡፡እያንዳንዱ ነገድ 1000 ለጦርነት የሚሰለፉ ሰዎችን ላከ፡፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:6

ኤዊ…ሮቆም…ሱር…ሑር…ሪባ

እነዚህ የምድያማውያን ነገሥታት ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የቢኦር ልጅ በለዓም

ቢኦር የበለዓም አባት ነበር፡፡ይህንን በዘኁልቁ 22፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 31:9

በዘበዙ

“የምድያማውያንን ንብረቶች የራሳችው አደረጉት”

ከተሞቻቸውን ሁሉ ሰፈሮቻቸውንም ሁሉ በእሣት አቃጠሉ

“እሥራኤላውያን ሠራዊቶች ምድያማውያን የሚኖሩባቸውን የምድያማውያንን ከተሞችና የምድያማውያንን ሠፈሮች ሁሉ አጠፉ”

Numbers 31:11

ወሰዱ

“የእሥራኤል ሠራዊት ወሰደው”

ብዝበዛው

ይሄ የሚያመለክተው ቁሳቁሶቹን ሁሉ በመውሰዳቸው ምክኒያት ምድያማውያንን ከሞት መታደጋቸውን ነው፡፡

ሜዳ

ሠፊ ሆኖ ለጥ ያለ መሬት፡፡

Numbers 31:13

ሻለቆችና የመቶ አለቆች

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/እነዚህ ቁጥሮች የሚያመለክቱት ሻለቆቹ ወይም የመቶ አለቆዎቹ የሚመሯቸው በሥራቸው የሚገኙ ሠራዊቶች ትክክለኛ ቁጥር ነው፡፡“1000 ሰራዊት የሚመሩ ሻለቃዎችና 100 ሠራዊት የሚመሩ መቶ አለቃዎች”ወይም 2/“ሺዎችና መቶዎች የሚሉት ቃላት የታላላቅና የአነስተኛ የጦር ክፍሎች ስያሜዎች ናቸው እንጂ የሠራዊቱን ትክክለኛ ቁጥር የሚያመለክቱ አይደሉም” “ሠፊ የጦር ክፍል ያላቸው ሻለቃዎችና አነስተኛ የጦር ክፍል ያላቸው መቶ አለቃዎች””(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በውኑ ሴቶችን ሁሉ አላዳናችኋቸውንም?

ማን ሊድን እንደሚገባና እንደፈሚቀድለት ሕጉ በግልፅ አስቀምጦታል፡፡ሠራዊቱ ግን ሕጉን በመፃረር ሰቶችንና ልጆችን በሕይወት እንዲኖሩ አድርገዋቸዋል፡፡ይሄ የሠራዊት መሪዎቹን ለመገሰፅ የቀረበ ጥያቄ ነው፡፡(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:16

ተመልከቱ

ይሄ ቃል እዚህ ሥፍራ ላይ ጥቅም ላይ እንዲውል የተደረገው ከዚህ በመቀጠል የሚነገረውን ነገር ሕዝቡ በጥሞና እንዲያዳምጥ ታስቦ ነው፡፡“አዳምጡ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከወንድ ጋር የተኛ

“ከወንድ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት ያደረገ”(ሥርዓት የሌለውን ነገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:18

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለእሥራኤል የጦር መሪዎች በእግዚአብሔር ፊት ንፁሕ መሆንን በተመለከተ ይነግራቸዋል፡፡

ከወንድ ጋር ተኝተን አናውቅም

ይሄ የሚያመለክተው ድንግል ሴቶችን ነው፡፡(ሥርዓት የሌለውን ነገር በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

ሁላችሁም

ሙሴ እዚሀ ላይ የሚናገረው የጦር አዛዦችን ብቻ ሣይሆን ማንኛውንም በጦርነቱ ላይ ተሣትፎ ያደረጉ ሰዎችን ሁሉ ነው፡፡

ራሣችሁን ማንፃት ይኖርባችኋል

ወደ ሠፈሩ ውስጥ ከመግባታቸው በፊት በመንፈሣዊ ሕይወታቸው ዳግም ንፁሕ ሊሆኑ ይገባል፡፡

ከቁርበት የተዘጋጀውን ሁሉ፤ከፍየልም ጠጉር፤ከእንጨትም የተሠራውን ሁሉ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“አንድ ሰው ከቁርበትከፍየልም ጠጉር፤ከእንጨትም የሠራውን ሁሉ” (ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:21

አጠቃላይ መረጃ

አልዓዛር ከሠልፍ የመጡትን ሰዎች ከጦርነት መልስ በኋላ በሕጉ ሥርዓት መሠረት እንዴት ንፁህ መሆን እንደሚገባቸው ያስተምራቸዋል፡

ወርቁን፤ብሩን፤ናሱን፤ብረቱን፤ቆርቆሮውን፤አረሩን

በዚያን ወቅት ጥቅም ላይ ይውሉ የነበሩ ብረቶች፡፡

በእሣት ውስጥ ለማለፍ የሚችለውን

“የማይቃጠለውን”

በእሣት ውስጥ ታሳልፉታላችሁ

“እሣት ውስጥ አሰቀምጡት”

የማንፃት ውኃ

ይሄ የሚያመለክተው አንድ ሰው ከኃጢአት ቁርባን የወሰደውን ውኃ ከአመድ ጋር የመደባለቁን ሁኔታ ነው፡፡(ኦሪት ዘኁልቁ 19፡17-19)

ከዚያ በኋላ ንፁህ ትሆናላችሁ

እነዚህ በሚከናወኑ ሥርዓቶች በእግዚአብሔር ፊት ንፁህ ሆኖ የመገኘት ልማዶች ናቸው፡፡

Numbers 31:25

የተማረኩትን ሁሉ ቁጠሩ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ወታደሮቹ የወሰዱትን ንብረት በሙሉ ቁጠሩ” (ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

የበዘበዛችሁት

ይሄ የሚያመለክተው እስራኤላውያን በጦርነት ውስጥ ከገደሏቸው ወይም ከማረኳቸው ሰዎች የወሰዷቸውን ንብረቶችን ነው፡፡

የማህበሩም አባቶች አለቆች

“የየነገዶቹ መሪዎች”

Numbers 31:28

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

አጠቃላይ መረጃ

“እኔ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ነው፡፡

ከእነዚያም ከተዋጉት ወደ ሠልፍም ከወጡት ለእኔ ያመጡ ዘንድ ቀረጥጣል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡“ወታደሮቹ ከማረኳቸው ነገሮች ላይ ቀረጥ በመጣል ለእኔ አምጣው፡፡(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከአምስት መቶ አንድ

“በየአምስት መቶው”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ከድርሻቸው

“ከወታደሮቹ ድርሻ”

ለእኔ ይሰጥ ዘንድ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እርሱ ለእኔ የሚሰጠውን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:30

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ከእሥራኤልም ሕዝብ ድርሻ

“የእሥራኤል ሕዝብ ከበዘበዘው ከግማሹ”

ከየሃምሳው

“ከየ50”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የሚጠብቁ

የመገናኛ ድንኳኑንና ለእግዚአብሔር የሚቀርቡትን መሥዋዕቶች በበላይነት የሚቆጣጠሩና የሚጠብቁ፡፡

Numbers 31:32

አሁን

ይሄ ቃል ጥቅም ላይ እንዲውል የተደረገውበዋናነት በሚሰጠው ትምህርት ላይ የተወሰነ እረፍት እንዳለ ለማሣየት ነው፡፡እዚህ ላይ ሙሴ ከተበዘበዙት ነገሮች ውስጥ ለወታደሮቹ፤ለሕዝቡና ለእግዚአብሔር ምን ያህል እንደተሰጠ ዝርዝራቸውን ያወጣል፡፡

675,000 በጎች

“ስድስት መቶ ሰባ አምስት ሺህ በጎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሁለት ሺህ በሬዎች፤ስድሳ ሺህ አህዮች፤ሠላሳ ሁለት ሺህ ሴቶች

“72,000 በሬዎች፤60 ሺህ አህዮችና 32,000 ሴቶች” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ወንድ የማያውቁ ሴቶች

ይሄ የሚያመለክተው ድንግል የሆኑ ሴቶችን ነው፡፡(ሥርዓት የሌለውን ቃል በመልካም ነገር መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:36

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ከተበዘበዙት ነገሮች ውስጥ ለወታደሮቹ የሚሰጠውንና ተቀርጦ ለእግዚአብሔር የሚሰጠውን ዝርዝር ማውጣት ይጀምራል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ይሄ በድርጊት መበዘመቻ ለነበሩ ሰዎች ድርሻ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለወታደሮቹ ከበጎቹ የሚደርሳቸው ድርሻ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

337,000 በጎች

“ሶስት መቶ ሰላሣ ሰባት ሺህ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

675 ነበር

“ስድስት መቶ ሰባ አምስት”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰላሣ ስድስት ሺህ

“36,000”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባ ሁለት

72(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:39

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ከተበዘበዙት ነገሮች ውስጥ ለወታደሮቹ የሚሰጠውንና ተቀርጦ ለእግዚአብሔር የሚሰጠውን ዝርዝር ማውጣት ይጀምራል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

30,500 ነበሩ

“ሰላሣ ሺህ አምስት መቶ ነበሩ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ስድሳ አንድ

61(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

አስራ ስድስት ሺህ

16,000(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰላሣ ሁለት

32 (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ለእግዚአብሔር ለግብርነት የሚሰጡ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ለእግዚአብሔር ቁርባን የሚሆነውን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:42

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ከተበዘበዙት ነገሮች ውስጥ ለወታደሮቹ የሚሰጠውንና ተቀርጦ ለእግዚአብሔር የሚሰጠውን ዝርዝር ማውጣት ይጀምራል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

337,500 በጎች

“ሶስት መቶ ሰላሣ ሰባት ሺህ አምስት መቶ በጎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰላሣ ስድስት ሺህ በሬዎች

“ሰላሣ ስድስት ሺህ በሬዎች”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

አሥራ ስድስት ሺህ ሴቶች

“16,000 ሴቶች”ቀደም ሲል እንደተጠቀሰው የተማረኩ ወንዶቹና ያገቡ ሴቶች በሙሉ በሕይወት እንዳይኖሩ ተደርጓል፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:47

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ከተበዘበዙት ነገሮች ውስጥ ለወታደሮቹ የሚሰጠውንና ተቀርጦ ለእግዚአብሔር የሚሰጠውን ዝርዝር ማውጣት ይጀምራል፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

አጠቃላይ መረጃ

በሕዝቡ ላይ የተጣለው ግብር በወታደሮቹ ላይ ከተጣለው ግብር ይልቅ ከፍ ያለ ነበር፡፡

Numbers 31:48

ሻለቆችና የመቶ አለቆች

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/እነዚህ ቁጥሮች የሚያመለክቱት ሻለቆቹ ወይም የመቶ አለቆዎቹ የሚመሯቸው በሥራቸው የሚገኙ ሠራዊቶች ትክክለኛ ቁጥር ነው፡፡“1000 ሰራዊት የሚመሩ ሻለቃዎችና 100 ሠራዊት የሚመሩ መቶ አለቃዎች”ወይም 2/ “ሺዎችና መቶዎች የሚሉት ቃላት የታላላቅና የአነስተኛ የጦር ክፍሎች ስያሜዎች ናቸው እንጂ የሠራዊቱን ትክክለኛ ቁጥር የሚያመለክቱ አይደሉም” “ሠፊ የጦር ክፍል ያላቸው ሻለቃዎችና አነስተኛ የጦር ክፍል ያላቸውመቶ አለቃዎች” ይህንንተመሳሳይ ሐረግ በዘኁልቁ 31፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ባሪያዎችህ ቆጥረናል

የሠራዊት አዛዦቹ ራሣቸውን “ባሪያዎችህ” እያሉ የጠሩት ከፍተኛ ሥልጣን ካለው ሰው ጋር ንግግር በሚደረግበት ወቅት ጥቅም ላይ የሚውል ትህትና ያለበት አቀራረብ ስለሆነ ነው፡፡

አንድ ሰው አልጎደለም

ይሄ በአዎንታዊ በሆነ አገላለፅ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሁሉም ሰው እዚህ እንደሚገኝ እርግጠኞች ነን”(በተዘዋዋሪ መንገድ ሃሣብን መግለፅ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 31:50

አጠቃላይ መረጃ

የሠራዊቱ አዛዦች ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላሉ፡፡

የእግር አልቦ፤አምባር፤ቀለበት፤ጉትቻ፤ድሪ

እነዚህ ሰዎች የሚያደርጓቸው ጌጣጌጦች ናቸው፡፡

በእግዚአብሔር ፊት ያስተሰርይልን ዘንድ

“ሕይወታችንን ስላዳነን እግዚአብሔርን እናመሰግን ዘንድ”

ወርቆቹንና በልዩ ልዩ የተሰራውን ዕቃ ሁሉ

“የወርቅ ዕቃዎችን ሁሉ”ወይም “የወርቅ ጌጣጌጦችን ሁሉ”

Numbers 31:52

ሻለቆችም የመቶ አለቆችም ለእግዚአብሔር የማንሣት ቁርባን ያቀረቡት ወርቅ ሁሉ አሥራ ስድስት ሺህ ሰባት መቶ ሰቅል ይመዝናል

“የሻለቆችቹና የመቶ አለቆቹ ለእግዚአብሔር የሰጡት የወርቅ ሥጦታ ሁሉ የመዘነው…”

ሻለቆችና የመቶ አለቆች

ለዚህ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/እነዚህ ቁጥሮች የሚያመለክቱት ሻለቆቹ ወይም የመቶ አለቆዎቹ የሚመሯቸው በሥራቸው የሚገኙ ሠራዊቶች ትክክለኛ ቁጥር ነው፡፡“1000 ሰራዊት የሚመሩ ሻለቃዎችና 100 ሠራዊት የሚመሩ መቶ አለቃዎች”ወይም 2/ “ሺዎችና መቶዎች የሚሉት ቃላት የታላላቅና የአነስተኛ የጦር ክፍሎች ስያሜዎች ናቸው እንጂ የሠራዊቱን ትክክለኛ ቁጥር የሚያመለክቱ አይደሉም” “ሠፊ የጦር ክፍል ያላቸው ሻለቃዎችና አነስተኛ የጦር ክፍል ያላቸው መቶ አለቃዎች” ይህንንተመሳሳይ ሐረግ በዘኁልቁ 31፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

16,750

“አሥራ ስድስት ሺህ ሰባት መቶ ሃምሳ”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ሰቅል

አንድ ሰቅል 11 ግራም ነው፡፡(መፅሐፍ ቅዱሣዊ ገንዘብ የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ፊት ለእሥራኤላውያን መታሰቢያ ይሆን ዘንድ

ወርቆቹ መታሰቢያ የሚሆኑት እግዚአብሔር ድል የሰጣቸው መሆኑን ለማሳሰብ ነው፡፡በሌላ በኩል ደግሞ በምድያማውያን ላይ ሕዝቡ የበቀል እርምጃ የወሰደ መሆኑን እግዚአብሔር ያስበው ዘንድ ነው፡፡


Chapter 32

1 በዚህ ጊዜ የሮቤልና የጋድ ትውልዶች ብዙ የቀንድ ከብቶች ነበራቸው፡፡ የኢያዜርንና የገለዓድን ምድር ሲመለከቱ፣ ምድሪቱ ለከብቶቻቸው መልካም መሆኗን አዩ፡፡ 2 ስለዚህ የጋድና ሮቤል ትውልዶች ወደ ሙሴ፣ ወደ ካህኑ አልዓዛርና ወደማህበሩ መሪዎች መጥተው እንዲህ አሉ፣ 3 “ያህዌ በእስራኤል ህዝብ ፊት የመታው አጣሮት፣ ዲቦን ኢያዜር፣ ኒምራ፣ ሐሴናን፣ ኤልያሊ፣ ሴባማ፣ ናባውና ባያን 4 ምድሩ ለከብቶች መልካም ነው፡፡ እኛ፣ የአንተ አገልጋዮች ብዙ ከበቶች አሉን፡፡” 5 ደግሞም እንዲህ አሉ፣ “በፊትህ ሞገስ አግኝተን ከሆነ፣ ይህች ምድር ለእኛ ለአገልጋዮችህ ርስት ሆና ትሰጠን፡፡ ዮርዳኖስን አቋርጠን እንድንሄድ አታድርግ፡፡” 6 ሙሴ ለጋድና ሮቤል ትውልዶች እንዲህ ሲል መለሰላቸው፣ “እናንተ በዚህ ተቀምጣችሁ ወንድሞቻችሁ ወደ ጦርነት ሊሄዱ ይገባልን? 7 የእስራኤል ህዝብ ያህዌ ወደ ሰጣቸው ምድር እንዳይገቡ ለምን ልባቸውን ታደክማላችሁ? 8 አባቶቻችሁ ከቀዴስ በርኔ ምድሪቱን እንዲያዩ በላክኋቸው ጊዜ ያደረጉት ተመሳሳይ ነገር ነበር፡፡ 9 እነርሱ ወደ ኤሽኮል ሸለቆ ሄዱ፡፡ ምድሪቱን ካዩ በኋላ የእስራኤልን ልብ አደከሙ፤ ስለዚህም ያህዌ ወደ ሰጣቸው ምድር ለመግባት ተቃወሙ፡፡ 10 በዚያ ቀን የያህዌ ቁጣ ነደደ፡፡ በመሀላ እንዲህ አለ፣ 11 ‘ከግብጽ ምድር ከወጡ ሰዎች ሃያ አመትና ከዚያ በላይ ከሆናቸው፣ መሃል አንዳቸውም ለአብርሃም፣ ለይስሃቅ፣ እና ለያዕቆብ ልሰጣቸው በመሀላ ቃል የገባሁላቸውን ምድር አያዩም፣ ምክንያቱም እነርሱ በሙሉ ልባቸው አልተከተሉኝም፤ 12 ከቂኔዛዊው ከዩፎኒ ልጅ ከካሌብ፣ እና ከነዌ ልጅ ከኢያሱ በስተቀር፡፡ ካሌብና ኢያሱ ብቻ በሙሉ ልባቸው ተከትለውኛል፡፡’ 13 ስለዚህም የያህዌ ቁጣ በእስራኤል ላይ ነደደ፡፡ በፊቱ ክፉ ያደረገው ትውልድ ሁሉ እስኪጠፋ ድረስ ለአርባ አመታት በምድረበዳ እንዲንከራተቱ አደረጋቸው፡፡ 14 እናንተ እንደ ሌሎች ኃጢአተኛ ሰዎች የያህዌን ቁጣ በእስራኤል ላይ ለመጨመር በአባቶቻችሁ እግር ተተካችሁ፡፡ 15 እርሱን ከመከተል ፊታችሁን ብታዞሩ፣ እርሱ እስራኤልን ዳግም በበረሃ ይተዋል እናንተም ይህን ሁሉ ህዝብ ታጠፋላችሁ፡፡” 16 ስለዚህም ወደ ሙሴ መጥተው እንዲህ አሉ፣ “በዚህ ለከብቶቻችን አጥር እና ለቤተሰቦቻችን ከተማ እንድንገነባ ፍቀድል፡፡ 17 ሆኖም፣ እኛ እራሳችን ወደ ስፍራቸው እስክናባርራቸው ድረስ ከእስራኤል ጦር ጋር ለመውጣት እንነሳለን እንታጠቃንም፡፡ ቤተሰቦችን ግን እስከ አሁን በዚህ ምድር ከሚኖሩ ሌሎች ሰዎች የተነሳ በተቀጠሩ ከተሞች ውስጥ ይኖራሉ፡፡ 18 የእስራኤል ህዝብ እያንዱ ሰው ርስቱን እስኪያገኝ ድረስ ወደ ቤቶቻችን አንመለስም፡፡ 19 እኛ ከእነርሱ ጋር ከዮርዳኖስ ማዶ ያለውን ምድር አንወርስም፣ ምክንያቱም የእኛ ርስት እዚህ በዮርዳኖስ ምስራቅ በኩል ያለው ነው፡፡” 20 ስለዚህም ሙሴ እንዲህ ሲል መለሰላቸው፣ “የተናገራችሁትን ካደረጋችሁ፣ ወደ ጦርነት በያህዌ ፊት ለመውጣት ራሳችሁን ካስታጠቃችሁ፣ 21 ከዚያ በኋላ እያንዳንዳቸው የእናንተ የታጠቁ ወንዶች ጠላቶቹን ከፊቱ እስኪያባርራቸው ድረስ በያህዌ ፊት ዮርዳኖስን ማቋረጥ አለባቸው፡፡ 22 ደግሞም ምድሪቱ በእርሱ ፊት ጸጥ ብላ ትገዛለች፡፡ ከዚያ በኋላ መመለስ ትችላላችሁ፡፡ እናንተም በያህዌና በእስራኤል ፊት ጥፋተኛ አትሆኑም፡፡ ይህ ምድር በያህዌ ፊት ርስታችሁ ይሆናል፡፡ 23 እንዲህ ካላደረጋችሁ ግን፣ በያህዌ ፊት በደለኞች ትሆናላችሁ ኃጢአታችሁ እንደሚከተላችሁ እርግጠኞች ሁኑ፡፡ 24 ለቤተሰቦቻችሁ ከተሞችን ገንቡ ለበጎቻችሁም ጉረነዎች ስሩላቸው፤ ከዚያ ያላችሁትን አድርጉ፡፡” 25 የጋድና ሮቤል ትውልዶች ሙሴን እንዲህ አሉት፣ “እኛ አገልጋዮችህ አንተ ጌታችን ያዘዝከንን እናደርጋለን፡፡ 26 ልጆቻችን፣ ሚስቶቻችን፣ መንጎችንና የቀን ከብቶቻችን በገለዓድ ከተሞች ይቆያሉ፡፡ 27 ሆኖም፣ እኛ፣ የአንተ አገልጋዮች ለጦርነት በያህዌ ፊት እንወጣን፤ ለጦርነት የታጠቀ እያንዳንዱ ሰው አንተ ጌታችን እንዳልከው ያደርጋል፡፡” 28 ስለዚህም ሙሴ ለካህኑ አልዓዛር፣ ለነዌ ልጅ ለኢያሱና በእስራኤል ህዝብ መሃል የጎሳዎች አባቶች ለሆኑ መሪዎች እነርሱን በሚመለከት መመሪያዎቻችን ሰጠ፡፡ 29 ሙሴ እንዲህ አላቸው፣ “የጋድና የሮቤል ትውልዶች ከእናንተ ጋር ዮርዳስን ቢሻገሩና በያህዌ ፊት ለጦርነት የታጠቀ እያንዳንዱ ወንድ እና ምድሪቱ በፊታችሁ ቢገዙ፣ የገለዓድን ምድር ለእነርሱ ርስት አድርገህ ትሰጣቸዋለህ፡፡ 30 ነገር ግን ታጥቀው ከአንተ ጋር ዮርዳኖስን ባይሻገሩ፣ ርስታቸውን በከነአን ምድር ከአንተ ጋር ያገኛሉ፡፡” 31 ስለዚህም የጋድና ሮቤል ትውልዶች እንዲህ ሲሉ መለሱ፣ “ያህዌ ለእኛ ለባሮችህ እንደተናገረው፣ የምናደርገው ነገር ይህ ነው፡፡ እንሻገራለን፡፡ 32 እኛ ታጥቀን በያህዌ ፊት ወደ ከነዓን ምድር እንሻገራለን፣ ነገር ግን የተወረሰው ርስታችን በዚህኛው የዮርዳስ ክፍል ከእኛ ጋር ይቀራል፡፡” 33 ስለዚህ ሙሴ ለጋድና ለሮቤል ትውልዶች፣ እንዲሁም ለዮሴፍ ልጅ ለምናሴ ከፊል ነገድ፤ የአሞውያንን ንጉስ የሴዎንን ግዛት እና የባሳንን ንጉስ የዓግን ግዛቶች ሰጣቸው፡፡ ለእነርሱ ምድሪቱን ሰጣቸው፣ እንዲሁም ከተማዎቿን ከዳርቻዎቻቸው ጋር እና በዙሪያቸው ያሉ ከተሞችን አደላቸው፡፡ 34 የጋድ ትውልዶች ዲቦንን፣ አጣሮትን፣ አሮዔርን፣ 35 ዓጥሮት ሾፋንን፣ አያዜርን፣ ዮግብሃን፣ 36 ቤት ነምራንን እና ቤት ሃራንን የተቀጠሩ ከተሞችና ለበጎች ጉረኖዎች ያላቸው አድርገው እንደገና ገነቧቸው፡፡ 37 የሮቤል ትውልዶች ሐሴቦንንና፣ ኤልያሊንና ቂርያትይምን፣ 38 ናባውን፣ በአልሜዎንን (ስማቸው በኋላ ተቀይሯል) እና ሴባማንን እንደገና ገነቧቸው፡፡ እነርሱም ዳግም ለገነቧቸው ከተሞች ሌላ ስሞችን ሰጡ፡፡ 39 የምናሴ ልጅ የማኪር ትውልዶች ወደ ገለዓድ ሄደው በውስጧ ይኖሩ ከነበሩት ከአሞራውያን ከለአድን ወሰዱ፡፡ 40 ከዚያ ሙሴ ለምናሴ ልጅ ለማኪር ገለዓድን ሰጠው፣ የእርሱም ሰዎች መኖሪያችን በዚያ አደረጉ፡፡ 41 የምናሴ ልጅ ኢያዕር ሄዶ ከተማቸውን ይዞ የኢያዕር መንደሮች ብሎ ሰየማቸው፡፡ 42 ኖባህ ሄዶ ቄናትንና መንደሮቿን ይዞ፣ በራሱ ስም ኖባህ ብሎ ሰየማት፡፡



Numbers 32:1

አሁን

ይሄ ቃል ጥቅም ላይ የዋለው በዋናው የታሪክ ሂደት ላይ የተወሰነ እረፍት እንዳለ ለማሣየት ነው፡፡እዚህ ላይ ሙሴ ስለ ሮቤልና ስለ ጋድ ነገዶች ስለጀርባ ታሪካቸው መረጃን ይሰጣል፡፡(የኋላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አጣሮት፤ዲቦን፤ኢያዜር፤ነምራ፤ሐሴቦን፤ኤልያሊ፤ሴባማ፤ናባው፤ባያን

እነዚህ የከተማዎቹ ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:4

አጠቃላይ መረጃ

ከሮቤልና ከጋድ የመጡ ሰዎች ለሙሴ፤ለአልዓዛርና ለሌሎቹ መሪዎች መናገራቸውን ይቀጥላሉ፡፡

እግዚአብሔር በእሥራኤል ማህበር ፊት የመታው ምድር

በዚያ ምድር የነበሩትን ሰዎች ድል እንዲያደርጓቸው እግዚአብሔር ችሎታውን የሰጣቸው ቢሆንም ልክ እግዚአብሔር ራሱ በእሥራኤላውያን ፊት ወጥቶ ጥቃት እንዳደረሰ ዓይነት ተድርጎ ተገልጿል፡፡“በዚያ የሚኖሩትን ሰዎች ድል እንደንነሳቻው እግዚአብሔር ችሎታውን ሰጠን” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ባሪያዎችህ

የሮቤልና የጋድ ሰዎች በዚህ መልክ ራሣቸውን የሚጠሩት ከፍ ያለ ሥልጣን ላለው ሰው አክበሮትን ለመሥጠት ነው፡፡

በዓይኖችህ ዘንድ ሞገስን አግኝተን እንደሆነ

እዚህ ላይ“ሞገስ” የሚለው ቃል ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ተቀባይነትን ማግኘት ወይም መሪዎቹ በእነርሱ ደስ መሰኘታቸውን የሚያሣይ ነው፡፡እዚህ ላይ “ዓይኖች”የሚለው ቃል እይታ ለሚለው ቃል ገላጭ ሲሆን እይታ ደግሞ የማመዛዘን ችሎታውን የሚያመለክት ምሣሌያዊ አነጋገር ነው፡፡“በአንተ ዘንድ ሞገስን አግኝተን ከሆነ”ወይም “በእኛ ደስ የተሰኘህ ከሆነ”(ፈሊጣዊ አነጋገር፤ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃልንና ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ርስት አድርገህ ስጠን

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ይህንን ምድር ለእኛ ስጠን”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ ዮርዳኖስም ማዶ አታሻግረን

የፈለጉት ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ተሻግረው መሬት መጠየቅ ሣይሆን ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምሥራቅ በኩል የሚገኘውን ሥፍራ ነበር የፈለጉት፡፡“በዚያኛ በኩል ለእኛ መሬትን ለመሥጠት ብለህ የዮርዳኖስ ወንዝን እንድሻገር አታድርገን”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:6

ወንድሞቻችሁ ወደ ጦርነት ሲሄዱ እናንተ እዚህ ትቀመጣላችሁን?

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው ሮቤልንና ጋድን ለመገሰፅ ብሎ ነው፡፡“ወንድሞቸችሁ ጦርነት ላይ እያሉ እናንተ በዚህ ምድር መቀመጣችሁ ተገቢ አይደለም”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

እግዚአብሔር የሰጣቸውን …..የሰውን ልብ ለምን ታደክማላችሁ?

ሙሴ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው ከሮቤልና ከጋድ ሃሣብ ሕዝቡን ለመከላከል ነው፡፡“እግዚአብሔር የሰጣቸውን ….. የሰውን ልብ አታድክሙ”ወይም “ድርጊታችሁ የሰዎችን ልብ ሊያደክሙ ይችላሉ….እግዚአብሔር የሰጣቸውን”(ምላሽ የማያሻው ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤልን ሕዝብ ልብ ከመሄድ ታደክሙታላችሁ

እዚህ ላይ“ልብ”የሚለው ቃል የሚወክለው ራሣቸው ሰዎቹን ሲሆን የሚያመለክተውም የስሜታቸው መሠረት የሆነውን ነገርነው፡፡“የእሥራኤል ሕዝብ እንዳይሄድ ተስፋ ታስቆርጡታላችሁ”ወይም “የእሥራኤል ሕዝብ እንዳይሄድ ምክኒያት ትሆናላችሁ”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:8

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ ለሮቤልና ለጋድ ሰዎች መናገሩን ይቀጥላል፡፡

የኤሽኮል ሸለቆ

ይሄ የቦታ ሥም ነው፡፡ይህንንበዘኁልቁ 13፡23 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሪቱን አዩ

ይሄ የሚያመለክተው በምድሪቱ ውስጥ ያለውን ነገር መመልከታቸውን ነው፡፡“በምድሪቱ ውስጥ የሚገኙትን ጠንካራ ሰዎችና ከተማዎቹን ተመለከቱ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤልን ልጆች ልብ አደከሙ

እዚህ ላይ“ልብ”የሚለው ቃል የሚወክለው ራሣቸው ሰዎቹን ሲሆን የሚያመለክተው የስሜታቸው መሠረት የሆነውን ነው፡፡ይህንንበዘኁልቁ 32፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡“የእሥራኤልን ሕዝብ ተስፋ አስቆረጡ”(ነገርን በተለየ መንገድ መረዳት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:10

የእግዚአብሔር ቁጣ ነደደ

x

Numbers 32:13

የእግዚአብሔርም ቁጣ በእሥራኤል ላይ ነደደ

እግዚአብሔር መናደዱን ለመግለፅ ልክ እሣት መቀጣጠል ከመጀመር ጋር ተመሳስሎ ነው የተነገረው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር በእሥራኤል ላይ በጣም ተናደደ”(ምሣሌያዊ አነጋገርና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

አርባ ዓመት

“40 ዓመት”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ትውልድ ሁሉ…ፊት እስኪጠፉ ድረስ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ትውልዱን ሁሉ አጠፋ…ፊት”ወይም “ትውልዱ ሁሉ…በእግዚአብሔር ፊት ጠፋ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በፊቱ ክፉ ያደረጉትን

በአንድ ሰው ፊት ማለት ሰውዬው ሊያየው በሚችልበት ሁኔታ ውስጥ መሆን ማለት ነው፡፡“በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ያደረገ”ወይም “የእግዚአብሔር ሕልውና ባለበት ክፉ ነገርን ያደረገ”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በአባቶቻችሁ ፋንታ ቆማችኋል

የሮቤልና የጋድ ሰዎች ልክ የአባቶቻቸውን ሥራ ማድረጋቸው አባቶቻቸው ባደረጉት ሥፍራ ላይ እንደቆሙ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እንደ አባቶቻችሁ ማድረግ ጀምራችኋል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔርን መዓት በእሥራኤል ላይ ትጨምሩ ዘንድ

ሰዎች እግዚአብሔር የበለጠ እየተናደደ እንዲሄድ የሚያደርጉት ድርጊት ልክ ሰዎች በእሣቱ ላይ ነዳጅ እንደሚጨምሩ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እግዚአብሔር በእሥራኤል ላይ የበለጠ እንዲናደድ ምክኒያት መሆን”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ይህንን ሁሉ ሕዝብ

“ይሄ ሁሉ ሕዝብ”ወይም“ይሄ ሁሉ ትውልድ”

Numbers 32:16

እንዘጋጃለን፤እንታጠቃለን

“መሣሪያችንን ታጥቀን ዝግጁዎች እንሆናለን”ወይም “በጦርነት ለመሣተፍ ዝግጁ እንሆናለን”

በተመሸጉ ከተሞች

“ደህንነታቸው በተጠበቁ ከተማዎች ውስጥ”

Numbers 32:18

አጠቃላይ መረጃ

ሮቤልና ጋድ መናገራቸውን እንቀጠሉ ነው፡፡

ርስቱን ወስዷል

ሰዎች እንደ ቋሚ ንብረት የሚቀበሉት ንብረት ልክ እንደሚወስዱት ንብረት ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“የሚደርሰውን የመሬት ድርሻ በንብረትነት ወስዷል”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:20

ራሣችሁን ብታስታጥቁ

“የጦር መሣሪያችሁን ብትወስዱ”

በእግዚአብሔር ፊት

የዚህ ትርጉም እግዚአብሔር በጦርነቱ ወቅት በፊታቸው በመሄድ ጠላቶቻቸውን ድል እንዲያደርጉ ጉልበትን በመሥጠት ምድራቸውን እንዲወርሱ ያደርጋል ማለት ነው፡፡(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ጠላቶቹን ከፊቱ እስኪያሳድድ ድረስ

እግዚአብሔር ጠላቶቹን ከፊቱ እስኪያሳድድ ድረስ፡፡እዚህ ላይ የሚገኙት ተውላጠ ስሞች ሁሉ የሚያመለክቱት እግዚአብሔርን ነው፡፡እግዚአብሔር ጠላቶቻቸውን ድል እንዲያደርጉ ያገዛቸውን ሁኔታ ልክ እግዚአበሔርየእነርሱን ጦርነት እየተዋጋ እንዳለ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“እግዚአብሔር ሠራዊቶቻችን ድል እንዲደርጓቸውና ከእርሱ ፊት እስኪዲያሳድዷቸው ድረስ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሪቱም በፊቱ ድል እስክትሆን ድረስ

እዚህ ላይ “ምድሪቱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው ኑሯቸውን በዚያ ያደረጉትን ሰዎች ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እሥራኤላውያን በዚያ ምድር የሚኖሩትን ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት ድል አደረጓቸው”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃልና ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ልትመለሱ ትችሉ ይሆናል

ይሄ የሚያመለክተው ከዮርዳኖስ በስተ ምሥራቅ በኩል ወደሚገኘው ሥፍራ የሚመለሱ መሆናቸውን ነው፡፡“ከዮርዳኖስ በስተ ምሥራቅ በኩል ወደሚገኘው ሥፍራ ልትመለሱ ትችሉ ይሆናል”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔርም ፊት በእሥራኤልም ዘንድ ንፁህ ትሆናላችሁ

ለዚህ ተስማሚ ፍቺ ሊሆኑ የሚችሉት 1/“የሚጠበቅባችሁን ግዴታ በእግዚአብሔርና በእራኤል ፊት ፈፅማችኋል”ወይም 2/“እግዚአብሔርም ሆነ የእሥራኤል ሕዝብ እናንተን የሚወቅሱበት ነገር የላቸውም”

Numbers 32:23

ኃጢአታእሁ እንዲያገኛችሁ እወቁ

ሙሴ በዚህ ሥፍራ ላይ ስለ ኃጢአት የሚናገረው ልክ አንድ ግለሰብ ጥፋተኛ የሆነን ሰው እንደሚኮንንዓይነት ነው፡፡ይሄ ማለት ሰዎች በሰሩት ኃጢአት ልክ ከመቀጣት አይድኑም ማለት ነው፡፡“እግዚአብሔር ስለ ኃጢአታችሁ እንደሚቀጣችሁ እርግጠኛ ሁኑ”(ግዑዝ ነገሮች ሕይወት እንዳላቸው ተደርገው ሲገለፁ የሚለውን ይመልከቱ)

ባሪያዎችህ

የጋድና የሮቤል ሰዎች ራሣቸውን “ባሪያዎችህ”እያሉ ነው የሚጠሩት፡፡ይሄ ከፍ ያለ ሥልጣን ላለው ሰው አክበሮት ለመሥጠት የሚውል ቃል ነው፡፡

Numbers 32:26

ይሻገራሉ

ዮርዳኖስን እንደሚሻገሩ ግልፅ ልታደርጉት ተችላላችሁ፡፡“የዮርዳኖስን ወንዝ ይሻገራሉ”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ለጦርነት ዝግጁ የሆነ ሰው ሁሉ

“በጦርነት ውስጥ ለመሣተፍ የተዘጋጀ ሰው ሁሉ”

Numbers 32:28

የጦር መሣሪ የታጠቀ ሰው ሁሉ

“የጦር መሣሪያውን ዝግጁ ያደረገ ሰው ሁሉ”

ምድሪቱንም ድል ብትነሱ

እዚህ ላይ “ምድሪቱ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው በዚያ የሚኖሩትን ሰዎች ነው፡፡ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በዚያ ምድር የሚኖሩትን ሰዎች እግዚአብሔርድል እንድትነሱ የሚያደርጋችሁ ከሆነ” ወይም “በምድሪቱ ውስጥ የሚኖሩትን ሰዎች ድል እንድታደርጓቸው እነርሱ የሚያግዟችሁ ከሆነ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

በከነዓን ምድር በእናንተ መካከል ርስታቸውን ይወርሳሉ

“የጋድና የሮቤል ትውልዶች በከነዓን ምድር ርታቸውን ይወርሳሉ”

Numbers 32:31

ትጥቃችንን እንደታጠቅን እንሻገራለን

ዮርዳኖስን እንደሚሻገሩ የበለጠ ግልፅ ልታደርጉት ትችላላችሁ፡፡“ዮርዳኖስን የምንሻገረው ለጦርነት ዝግጁ ሆነን ነው”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የምንወስደው ርስታችን

ሕዝቡ እንደ ቋሚ ንብረትነት የሚወስደውን መሬት በውርስ እንደሚወስዱት ዓይነት ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡“የራሣችን የምናደርገው የመሬት ድርሻችን” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የእኛ ይሆናል

ይሄ ፈሊጣዊ አጋገር የሚያመለክተው የራስ ንብረት ማድረግን ነው፡፡“የራሣችን ይሆናል”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:33

የሴዎን ግዛትና…የዐግ

እነዚህ ሁለት የተለያዩ ግዛቶችን የገዙ ነገሥታት ሥሞች ናቸው፡፡“የሴዎን ግዛትና…የዐግ ግዛት”(ምልክቶች እንጂ ቃላት ጥቅም ላይ የማይውሉበት የሚለውንና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:34

ዲቦን፤አጣሮት፤አሮኤል፤ዓጥሮትፋሽፋን፤ኢያዜር፤ዮግብሃን፤ቤትነምራነና

እነዚህ የከተሞች ሰሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 32:37

ሐሴቦን፤ኤልያሊ፤ቂርያታይም፤ናባው፤በኣልሜዎን..ሴባማ

እነዚህ የከተሞች ሰሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

በኋላ ላይ ስማቸው ተለወጠ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በኋላ ላይ ሰዎች የእነዚሀን ከተሞች ስሞች ለወጧቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ማኪር

ይሄ የሰው ሥም ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 26፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 32:40

ኢያዕር…ኖባህ

እነዚህ የሰዎች ሰሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)አ

ኢያዕር…ቄናት

እነዚህ የከተሞች ሰሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 33

1 የእስራኤል ህዝብ በሙሴና አሮን መሪነት በየታጣቂ በድኖቻቸው ሆነው ከግብጽ ምድር ከወጡ በኋላ ያደረጓቸው ጉዞዎች እነዚህ ነበሩ፡፡ 2 ሙሴ በያህዌ እንደታዘዘው፣ ከተነሰቡት አንስቶ እስሚሄዱበት ድረስ ያሉትን ስፍራዎች ጻፈ፡፡ ከስፍራ ስፍራ ያደረጓቸው እንቅስቃሴዎች እነዚህ ነበሩ፡፡ 3 በመጀመሪያው ወር፣ በወሩ በአስራ አምስተኛ ቀን ከራምሴ ተነስተው ተጓዙ፡፡ ከፋሲካው በኋላ በማለዳ፣ የእስራኤል ሕዝብ በግልጽ ግፃዊያን ሁሉ እያይዋቸው ወጡ፡፡ 4 ግብፃዊያን ያህዌ በመካከላቸው የገደላቸውን በኩሮቻቸውን እየቀበሩ ሳለና በአማልክቶቻቸው ላይ ጥፋት እያደረሰ ሳለ ይህ ሆነ፡፡ 5 የእስራኤል ሕዝብ ከራምሴ ወጥቶ በሱኮት ሰፈረ፡፡ 6 ከሱኮት ወጥተው በኤታሞ፣ በምድረ በዳው 7 ከኤታም ወጥተው ከበአልዛፎን በተቃራኒ ወደ ፊሀሔርት ተመልሰው በሚግዶል በተቃራኒ ሰፈሩ፡፡ 8 ከዚያም ከፈሀሔርት በተቃራኒ ተነስተው በባህሩ መሃል ወደ ምድረበዳው ሄዱ፡፡ ለሶስት ቀናት በኤታም ምድረ በዳ ተጉዞው በማራ ሰፈሩ፡፡ 9 ከማራ ተነስተው ኤሊም ደረሱ፡፡ በኤሊም አስራ ሁለት ምንጮችና ሰባ የቴምር ዛፎች ነበሩ፡፡ የሰፈሩት በዚያ ስፍራ ነው፡፡ 10 ከኤሊም ተነስተው ቀይ ባህር አጠገብ ሰፈሩ፡፡ 11 ከቀይ ባህር ተነስተው በሲን ምድረበዳ ሰፈሩ፡፡ 12 ከሲን ምድረበዳ ተነስተው በራፍቃ ሰፈሩ፡፡ 13 ከራፍቃ ተነስተው በኤሉስ ሰፈሩ፡፡ 14 ከኤሉስ ተነስተው የሚጠጣ ውሃ በሌለበት ሰራፊዲም ሰፈሩ፡፡ 15 ከራፊዲም ተነስተው በሲና ምድረበዳ ሰፈሩ፡፡ 16 ከሲና ምድረበዳ ተነስተው በቂብሮት ሃታቫ ሰፈሩ፡፡ 17 ከቂብሮት ሃታቫ ተነስተው በሐዴሮት ሰፈሩ፡፡ 18 ከሐዴሮት ተነስተው በሪትማ ሰፈሩ፡፡ 19 ከሪትማ ተነስተው በሬሞን ዘፋሬስ ሰፈሩ፡፡ 20 ከሬምን ዘፋሬስ ተነስተው በልብና ሰፈሩ፡፡ 21 ከልብና ተነስተው በሪሳ ሰፈሩ፡፡ 22 ከሪሳ ተነስተው በቀሄላታ ሰፈሩ፡፡ 23 ከቀሄላታ ተነስተው በሻፍር ተራራ ሰፈሩ፡፡ 24 ከሻፍር ተራራ ተነስተው በሐራዳ ሰፈሩ፡፡ 25 ከሐራዳ ተነስተው በመቅሄሎት ሰፈሩ፡፡ 26 ከመቅሄሎት ተነስተው በታሐት ሰፈሩ፡፡ 27 ከታሐት ተነስተው በታራ ሰፈሩ፡፡ 28 ከታራ ተነስተው በሚትቃ ሰፈሩ፡፡ 29 ከሚትቃ ተነስተው በሐሹምና ሰፈሩ፡፡ 30 ከሐሽምና ተነስተው በምሴሮት ሰፈሩ፡፡ 31 ከሞሴሮት ተነስተው በብኔያዕቃን ሰፈሩ፡፡ 32 ከብኔያዕቃን ተነስተው በሖር ሃጊድጋድ ሰፈሩ፡፡ 33 ከሖር ሃጊድጋ ተነስተው በዮጥባታ ሰፈሩ፡፡ 34 ከዮጥባታ ተነስተው በዔብሮና ሰፈሩ፡፡ 35 ከዔብሮና ተነስተው በዔድዮን ጋብር ሰፈሩ፡፡ 36 ከዔድዮን ጋብር ተነስተው በቃዴስ በምትገኘው ጺን ምድረ በዳ ሰፈሩ፡፡ 37 ከቃዴስ ተነስተው በሖር ተራራ፣ በኤዶም ምድር ዳርቻ ሰፈሩ፡፡ 38 ካህኑ አሮን፤ በያህዌ ትዕዛዝ ወደ ሖር ተራራ ወጣ፣ የእስራኤል ህዝብ ከግብጽ ምድር በወጣበት በአርባኛው ዓመት፣ በአምስተኛው ወር፣ በወሩ በመጀመሪያው ቀን ካህኑ አሮን በዚያ ሞተ፡፡ 39 አሮን በሖር ተራራ ላይ ሲሞት ዕድሜው 123 ነበር፡፡ 40 በከነዓን ምድር በደቡባዊ በረሃ የሚኖረው ከነዓናዊው የዓራድ ንጉስ የእስራኤልን ህዝብ መምጣት ሰማ፡፡ 41 እነርሱ ከሖር ተራራ ተነስተው በሴልምና ሰፈሩ፡፡ 42 ከሴልምና ተነስተው በፋኖን ሰፈሩ፡፡ 43 ከፋኖን ተነስተው በአቦት ሰፈሩ፡፡ 44 ከአቦት ተነስተው በሞአብ ዳርቻ በኢየ አባሪም ሰፈሩ፡፡ 45 ከኢየ አባሪም ተነስተው በዲቦን ጋድ ሰፈሩ፡፡ 46 ከዲቦን ጋድ ተነስተው በዓልምን ዲብላታይም ሰፈሩ፡፡ 46ከዲቦን ጋድ ተነስተው በዓልምን ዲብላታይም ሰፈሩ፡፡ 47 ከዓልምን ዲብላታይም ተነስተው ከናባው ተራራ በተቃራኒ በዓብሪም ተራራ ሰፈሩ፡፡ 48 ከዓብሪም ተራራ ተነስተው በሞብ ሜዳዎች በዮርዳኖስ ኢያሪኮ ላይ ሰፈሩ፡፡ 49 በሞብ ሞአብ ዮርዳስ ላይ ከቤት የሺሞት እስከ አቤልስጢም ድረስ ሰፈሩ፡፡ 50 ያህዌ ሙሴን በሞአብ ሜዳዎች ዮርዳስ ውስጥ በኢያሪኮ ሳለ እንዲህ አለው፣ 51 “ለእስራኤላዊያን እንዲህ በላቸው፣ ‘ዮርዳኖስን አቋርጣችሁ ወደ ከነዓን ስትገቡ፣ 52 የምድሪቱን ነዋሪዎች በሙሉ ከፊታችሁ አስወጡ፡፡ የተቀረጹ ምስሎቻቸውን በሙሉ አጥፉ፡፡ የማምለኪያ ስፍራዎቻቸውንና የተቀረጹ ምስሎቻቸውን ሁሉ ደምስሱ፡፡ 53 የምድሪቱን ሀብት ውሰዱ በዚያም መኖር ጀምሩ፣ ምክንያቱም እኔ ምድሪቱን ለእናንተ ርስት አድርጌ ሰጥቻቸኋለሁ፡፡ 54 ምድሪቱን በእጣ እንደየ ጎሳው ብዛት ውረሱ፡፡ ብዙ ህዝብ ላለው ጎሳ ሰፊ መሬት ስጥ፣ አነስተኛ ቁጥር ላለው ጎሳ አነስ ያለ መሬት ስጥ፡፡ እያንዳንዱ ጎሳ እጣው በወደቀለት ስፍራ ያ መሬት ርስቱ ይናል፡፡ ምድሪቱን በአባቶችሁ ጎሳ መሰረት ትወርሳላችሁ፡፡ 55 የምድሪቱን ነዋሪዎች ከፊታችሁ ጨርሳችሁ ባታስወጡ ግን፣ እንዲቀሩ ያደረጋችኋቸው ሰዎች በዐይናችሁ ውስጥ እንደገባ ባዕድ አካል እና በጎናችሁ እንደገባ እሾህ ይሆኑባችኋል፡፡ በመትኖሩበት ምድር ሕይወታችሁን ከባድ ያደርጉባችኋል፡፡ 56 እኔ በእነዚህ ህዝቦች ላይ ላደርስባቸው ያቀድኩትን በእናንተም ላይ ደግሞ አደርገዋለሁ፡፡’”



Numbers 33:1

ከታጠቁ ጭፍሮቻቸው በታች

“በየጦር ክፍሎቻቸው” “ይሄ የሚያሣየው እያንዳንዱ ነገድ የታጠቁና ከጠላት የሚከላከሉላቸው የራሣቸው ሰዎች ነበሯቸው ማለት ነው”“የታጠቀ ሠራዊት”የሚለውን ሐረግ በዘኁልቁ 1፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

በእግዚአብሔር ትዕዛዝ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ጉዟቸው፤አወጣጣቸው

“ከአንድ ሥፍራ ወደ ሌላ ሥፍራ”

Numbers 33:3

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

በመጀመሪያው ወር ከወሩም በአሥራ አምስተኛው ቀን ተጓዙ

“በመጀመሪያ”የሚለው ተከታታይ ቄጥር የሆነው አንድ ሲሆን “በአሥራ አምስተኛው”የሚለው ደግሞ ተከታታይ ቁጥር የሆነው አሥራ አምስት ነው፡፡ይሄ ለዕብራውያን የመጀመሪያው ወራቸው ነው፡፡በምዕራባውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት አሥራ አምስተኛው ቀን የሚውለው በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ ነው፡፡(የዕብራውያን ቀን አቆጣጠርናተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል ልጆች ግብፃውያን ሁሉ እያዩ ከፍ ባለች እጅ ወጡ

“እሥራኤላውያን ከግብፃውያን ሳይደበቁ ፊት ለፊት እያይዋቸው ወጡ”

በኩሮቻቸው

ይሄ የሚያመለክተው በኩር የሆኑ ወንድ ልጆችን ነው፡፡“በኩር ወንድ ልጆቻቸውን”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በአማልክቶቻቸውም ደግሞ ፈረደባቸው

እግዚአብሔር በግብፅ ከሚመለኩት ጣዖታት ይልቅ እጅግ ኃያል እንደሆነ የሚያረጋግጠውን ነገር ልክ እግዚአብሔር ጣዖቶቻቸውን እንደቀጣ ዓይነት ተደርጎ ተገልጿል፡፡“ከጣዖቶቻቸው ይልቅ ኃያል እንደሆነ አረጋገጠ”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:5

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ከሆነ ሥፍራ ወጡ

“ከሆነ ቦታ ለቀቁ”

በምድረ በዳው ጫፍ

“በምድረው በዳ ድንበር”

Numbers 33:8

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

በባህሩ ውስጥ አለፉ

ይሄ የሚያመለክተው እሥራኤላውያን ከግብፃውያን ሠራዊት ያመልጡ ዘንድ እግዚአብሔር ቀይ ባህርን የከፈለበትን ሁኔታ ነው፡፡

አሥራ ሁለት የውኃ ምንጮች…ሰባ ዘንባቦች

“12 የውኃ ምንጮች…70 ዘንባቦች”(ቁጥሮች የሚለውን ተመልከቱ)

Numbers 33:11

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ሕዝቡ የሚጠጠው ውኃ አልነበረውም

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ሰዎች ውኃ ለማግኘት የተቸገሩበት ሁኔታ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:15

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:19

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:23

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:27

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:31

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:35

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:38

ከአርባኛው ዓመት በኋላ

“ከአርባኛው”የሚለው ቃል አርባ ለሚለው ቁጥር ተከታታይነትን የሚያመለክት ነው፡፡“ከ40 ዓመት በኋላ” (ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

በአምስተኛው ወር ከወሩም በመጀመሪያው ቀን

“አምስተኛው”የሚለው ቃል አምስት ለሚለው ቁጥር ተከታታይነትን የሚያመለክት ነው፡፡“በዕብራውያን አቆጣጠር መሠረት ይሄ አምስተኛው ወር ነው”በምዕራባውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት የመጀመሪያው ቀን የሚውለው ሐምሌ መሐል አካባቢ ነው፡፡(የዕብራውያን ቀን አቆጣጠርንና ተከታታይነት ያለው ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ዕድሜው 123 ዓመት

“መቶ ሃያ ሶስት ዓመት”(ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:40

ከነዓናዊው የዓራድ ንጉሥ

“የዓራድ ከነናዊ ንጉሥ”(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

አራድ

ይሄ የከነዓናውያን ከተማ ሥም ነበር፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የእሥራኤል ልጆች እንደመጡ ሰማ

“የእሥራኤል ልጆች እየመጡ እንደሆነ ወሬ ሰማ”

Numbers 33:41

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:44

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 33:47

አጠቃላይ መረጃ

ሙሴ እሥራኤላውያን ከግብፅ ምድር ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ የተጓዙባቸውን የቦታዎች የሥም ዝርዝር መፃፍ ይጀምራል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ሜዳ

ሠፊ የሆነና ለጥ ያለ መሬት

Numbers 33:50

ከፍ ያሉ ሥፈራዎቻቸውን ሁሉ ታፈርሳላችሁ

“ከፍ ያሉ ሥፈራዎቻቸውን ሁሉ ታፈርሳላችሁ”

Numbers 33:53

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሕዝቡ ምን ማድረግ እንደሚኖርበት ለሙሴ እየተናገረ ነው፡፡

ምድሪቱን መውረስ

ሕዝቡ እንደ ቋሚ ንብረትነት የሚወስደውን መሬት በውርስ እንደሚወስዱት ዓይነት ተደርጎ ነው የተገለፀው፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሪቱንም በየወገኖቻችሁ በዕጣ ትወርሳላቸሁ

“እያንዳንዱ ነገድ በሚወጣለት ዕጣ መሠረት መሬቱን ይረከባል”

Numbers 33:55

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሕዝቡ ምን ማድረግ እንደሚኖርበት ለሙሴ እየተናገረ ነው፡፡

ለዓይናችሁ እንደ እሾህ ለጎናችሁም እንደሚወጋ ነገር

በአንድ ሰው ወስጥ ትንሽ ነገር ዓይኑ ውስጥ ቢገባ ወይም ትንሽ እሾህ በሰው ቆዳ ውስጥ ቢገባ እንደሚያበሳጭ ሁሉ ከከነዓናውያን መካከል የተወሰኑ ሰዎች በምድሪቱ ላይ ቢቀሩ ለእሥራኤላውያን ትልቅ ችግርን ሊፈጥሩ ይችላሉ፡፡(ተነፃፃሪ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 34

1 ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 2 “የእስራኤልን ሰዎች እንዲህ ብለህ እዘዛቸው፣ ‘የእናንተ ወደምትሆን የከነዓን ምድርና ወደ ድንበሮቿ ስትገቡ፣ 3 ደቡባዊ ድንበራችሁ ከሲና ምድረ በዳ እስከ ኤዶም ይደርሳል፡፡ የደቡባዊ ድንበር ምስራቃዊ ጫፍ በጨው ባህር ደቡባዊ ጫፍ ድረስ ይሆናል፡፡ 4 ከአቅራቢም ኮረብታ ድንበራችሁ ወደ ደቡብ ይዞርና በሲና ምድረበዳ በኩል ያልፋል፡፡ ከዚያ ተነስቶ፣ በቃዴስ በርኔ ደቡብ ያልፍና ወደ ሐጸር አዳር እና ርቆ ዓጽምን ይደርሳል፡፡ 5 ከዚያ ተነስቶ፣ ድንበሩ ከጽሞን ወደ ግብጽ ጅረት ዞሮ እስከ ባህሩ ይከተለዋል፡፡ 6 ምዕራባዊው ድንበር የታላቁ ባህር ዳርቻ ይሆናል፡፡ ይህ ምዕራባዊ ድንበራችሁ ይሆናል፡፡ 7 ሰሜናዊ ድንበራችሁ ከታላቁ ባህር እስከ ሆር ተራራ እስከ ምትይዙት ስፍራ ድረስ ይሰፋል፣ 8 ከዚያ ከሖር ተራራ እስከ ሌና ሐማት፣ ከዚያ እስከ ጽዳድ ይደርሳል፡፡ 9 ከዚያ ድንበሩ እስከ ዚፍሮን ይቀጥልና ሐጻር ዔርን ሲደርስ ይጨርሳል፡፡ ይህ ሰሜናዊ ድንበራችሁ ይሆናል፡፡ 10 ምስራቃዊ ድንበራችሁን ከሐጸር ዔናን በደቡብ እስከ ሴፋም ታደርጋላችሁ፡፡ 11 ምስራቃዊ ድንበራችሁ ታች እስከ ሴፋም ወርዶ በዓይን ምስራቅ በኩል ራብላ ይደርሳል፡፡ ድንበሩ እስከ ከኔሬት ባህር ምስራቅ ይዘልቃል፡፡ 12 ከዚያ ድንበሩ በደቡብ በዮርዳኖስ ወንዝ በኩል እስከ ጨው ባህር እና ታች የጨው ባህር ምስራቅ ዳርቻ ድረስ ይቀጥላል፡፡ ይህች ድንበሩን ተከትሎ ዙሪያውን በሙሉ የእናንተ ምድራችሁ ናት፡፡ 13 ሙሴ የእስራኤልን ሰዎች እንዲህ ሲል አዘዘ፣ “ያህዌ ለዘጠኙ ጎሳዎችና ለአንዱ ጎሳ እኩሌታ እንዲሰጣችሁ ያዘዘው፣ በዕጣ የምትካፈሏት ምድር ይህች ናት፡፡ 14 የሮቤል ጎሣ ትውልዶች እና የጋድ ጎሣ ትውልዶች እንዲሁም የምናሴ ነገድ እኩሌታ በየአባቶቻቸው ጎሣዎች የንብረት አከፋፈልን ስርዓት ተከትለው ርስታቸውን ተቀብለዋል፡፡ 15 ሁለቱ ጎሣዎችና የአንዱ ጎሣ እኩሌታ ከዮርዳኖስ ወዲያ በኢያሪኮ በስተ ምስራቅ በጸሀይ መውጫ የርስታቸውን ድርሻ ተቀብለዋል፡፡” 16 ያህዌ ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፣ 17 “ምድሪቱን ርስታችሁ አድርገው የሚያፋፍሏችሁ ሰዎች ስማቸው እነዚህ ናቸው፡ ካህኑ አልዓዛርና የነዌ ልጅ ኢያሱ ናቸው፡፡ 18 ለየጎሣቸው ምድሪቱን እንዲያካፍሉ ከየነገዱ አንድ መሪ ምረጡ፡፡ 19 የሰዎቹም ስሞች እነዚህ ናቸው፡ ከይሁዳ ነገድ የዩፎኒ ልጅ ካሌብ፡፡ 20 ከስምኦን ጎሣ ትውልዶች የዓሁድ ልጅ ሰላሚኤል፡፡ 21 ከቢኒያም ጎሣ፣ የኪስሎን ልጅ ኤልዳድ፡፡ 22 መሪ ከሆነው ከዳን ጎሣ ትውልዶች፣ የዩግሊ ልጅ ቡቂ፡፡ 23 ከዮሴፍ ትውልዶች፣ መሪ ከሆነው ከምናሴ ትውልዶች የሱፊድ ልጅ አኒኤል፡፡ 24 መሪ ከሆነው ከኤፍሬም ጎሣ ትውልዶች፣ የሺፍጣን ልጅ ቱሙኤል፡፡ 25 መሪ ከሆነው ከዛብሎን ጎሣ ትውልዶች የፈርናክ ልጅ ኤሊሳፈን፡፡ 26 መሪ ከሆነው ከይሳኮር ጎሣ ትውልዶች፣ የሖዛ ልጅ ፈልጢኤል፡፡ 27 መሪ ከሆነው ከኤሴር ጎሣ፣ የሴሌሚ ልጅ አሒሁድ፡፡ 28 መሪ ከሆነው ከንፍታሌም ጎሳ ትውልዶች፣ የዓሚሁድ ልጅ ፈዳሄል” ናቸው፡፡ 29 ያህዌ እነዚህን ሰዎች የከነዓንን ምድር እንዲያካፍሉና ለእያንዳንዱ የእስራኤል ጎሣዎች ድርሻቸውን እንዲሰጡ አዘዘ፡፡



Numbers 34:1

የጺን ምድረ በዳ

ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 33፡12 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 34:4

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሙሴ ለእሥራኤላውያን የሚሰጠው መሬት ድንበሩ የት እንደሆነ ይነግረዋል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 34:6

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሙሴ ለእሥራኤላውያን የሚሰጠው መሬት ድንበሩ የት እንደሆነ ይነግረዋል፡፡

Numbers 34:7

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሙሴ ለእሥራኤላውያን የሚሰጠው መሬት ድንበሩ የት እንደሆነ ይነግረዋል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

የሖር ተራራ

ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 20፡22 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡

Numbers 34:10

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሙሴ ለእሥራኤላውያን የሚሰጠው መሬት ድንበሩ የት እንደሆነ ይነግረዋል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 34:13

ለዘጠኝ ነገድ ተኩል

ይሄ ማለት በከነዓን ምድር ከዮርዳኖስ በስተ ምዕራብ በኩል ወደፊት የሚኖሩት የእሥራኤል የቀሩት ነገዶች ናቸው፡፡የሮቤል፤የጋድና ግማሹ የምናሴ ነገድ መሬታቸውን ከዮርዳኖሰ በስተ ምሥራቅ በኩል ተቀብለዋል፡፡

በየአባቶቻቸው ቤት የርስት ምደባ መሠረት

“እግዚአብሔር ንብረቱን ለአባቶቻቸው ቤት በመደበው መሠረት”

ሁለቱ ነገድና የአንዱ ነገድ እኩሌታ

“የሮቤልና የጋድ ነገዶችና ግማሹ የምናሴ ነገድ”

Numbers 34:16

ለእናንተ ርስት እንዲሆን ምድሪቱን ክፈል

እዚህ ላይ “እናንተ”የሚለው ቃል የብዙ ቁጥር ሲሆን የሚያመለክተውም የእሥራኤልን ሕዝብ ነው፡፡እነዚህ ሰዎች መሬቱን ለመከፋፈል ዕጣ ይጥላሉ፡፡ከዚያ በኋላ በየነገዶቹ ያከፋፍሉታል፡፡(እናንተ የሚለውን የተለያየ አገላለፆች ይመልከቱ)

Numbers 34:19

አጠቃላይ መረጃ

ለየነገዶቹ መሬቱን ለማከፋፈል እገዛ የሚያደርጉት ሰዎች የሥም ዝርዝር እነዚህ ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 34:21

አጠቃላይ መረጃ

ለየነገዶቹ መሬቱን ለማከፋፈል እገዛ የሚያደርጉት ሰዎች የሥም ዝርዝር እነዚህ ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 34:24

አጠቃላይ መረጃ

ለየነገዶቹ መሬቱን ለማከፋፈል እገዛ የሚያደርጉት ሰዎች የሥም ዝርዝር እነዚህ ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 34:27

አጠቃላይ መረጃ

ለየነገዶቹ መሬቱን ለማከፋፈል እገዛ የሚያደርጉት ሰዎች የሥም ዝርዝር እዚህ ላይ ይጠናቀቃል፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 35

1 ያህዌ ሙሴን በሞአብ ሜዳ ዮርዳኖስ አጠገብ በኢያሪኮ እንዲህ አለው፣ 2 ”የእስረኤል ሰዎችን ለሌዋውያን ርስታቸው ከሆነው ከድርሻቸው እንዲሰጧቸው እዘዝ፡፡ የሚኖሩባቸውን ከተሞችና በዙሪያቸውም የግጦሽ መሬት ይስጧቸው፡፡ 3 ሌዋውያን እነዚህን ከተሞች መኖሪያቸው ያድርጓቸው፡፡ የግጦሽ መሬቱ ለከብቶቻቸው ለመንጎቻቸው እና ለእንስሳቻቸው ይሁኑ፡፡ 4 ለሌዋውያኑ የምትሰጣቸው በከተሞቹ ዙሪያ የሚገኘው የግጦሽ መሬት ከከተማ ቅጥር በየአቅጣጫው ስፋቱ አንድ ሺህ ክንድ ይሆናል፡፡ 5 ከከተማዋ በምስራቅ አቅጣጫ ሁለት ሺህ ክንድ ለካ፣ በስተደቡብ በኩልም ሁለት ሺህ ክንድ ለካ፣ በምዕራብ በኩል ሁለት ሺህ ክንድ፣ እና በሰሜን በኩል ሁለት ሺህ ክንድ ለካ፡፡ ይህ በከተማቸው ዙሪያ የግጦሽ መሬት ይሆናል፡፡ ከተማይቱ በመሃል ትሆናለች፡፡ 6 ለሌዋውያን የምትሰጧቸው ስድስቱ ከተሞች የስደተኞች ከተሞች ሆነው ያገለግሉ፡፡ እነዚህን ከተሞች በነፍስ መግደል ለተከሰሱ መሸሻ ስፍራ እንዲሆኑ ስጣቸው፡፡ እንዲሁም ሌሎች አርባ ሁለት ከተሞችን ስጣቸው፡፡ 7 ለሌዋውያን የምትሰጣቸው ከተሞች በጠቅላላው አርባ ስምንት ይሆናሉ፡፡ ከከተሞቹ ጋር የግጦሽ መሬትም ትሰጣቸዋለህ፡፡ 8 ብዙ የሆኑ የእስራኤል ህዝብ ጎሳዎችና ብዙ መሬት ያላቸው ጎሣዎች ብዙ ከተሞች ይሰጣቸዋል፡፡ አነስተኛዎቹ ጎሣዎች ጥቂት ከተሞች ይሰጣቸዋል፡፡ እያንዳንዱ ነገድ እንደ ተቀበለው እንደ ድርሻው መጠን ለሌዋውያኑ መስጠት አለበት፡፡” 9 ከዚያም ያህዌ ሙሴን እንዲህ አለው፣ 10 “ለእስራኤል ሰዎች እንዲህ በላቸው፣ ‘ዮርዳኖስን አቋርጣችሁ ወደ ከነዓን ስትገቡ፣ 11 ይሁነኝ ብሎ ሰው ያልገደለ ሰው ወደ እነዚያ ከተሞች መግባት እንዲችል የመሸሸጊየ ከተማ ሆነው የሚያገለግሉ ከተሞችን ምረጡ፡፡ 12 እነዚህ ከተሞች ከደመኞቻችሁ የምትሸሸጉባቸው ይሁኑ፣ ስለዚህም የተከሰሰው ሰው በቅድሚያ በማህበሩ ፊት ለፍርድ ሳይቀርብ አይገደልም፡፡ 13 የመሸሸጊያ ከተማ አድርጋችሁ ስድስት ከተሞችን ምረጡ፡፡ 14 ከዮርዳኖስ ወዲያ ሶስት ከተሞችን፣ በከነዓን ምድር ደግሞ ሶስት ከተሞችን ስጡ፡፡ እነዚህ የመሸሸጊያ ከተሞች ይሆናሉ፡፡ 15 እነዚህ ስድስት ከተሞች ለእስራኤል ሰዎች፣ ለመጻተኞች፣ እና ለማናቸውም በመሀላቸው ለሚኖር ሳያውቅ ሰውን ለገደለ መሸሸጊያ ሆነው ያገለግላሉ፡፡ 16 ነገር ግን የተከሰሰው ሰው ተበዳዩን በብረት መሳሪያ ቢመታውና ተጠቂው ቢሞት፣ ተከሰሹ ነፍሰ ገዳይ ነው፡፡ እርሱ በእርግጥ ይገደል፡፡ 17 የተከሰሰው ሰው በእጁ በያዘው ድንጋይ ተበዳዩን ቢመታና ተበዳዩ ቢሞት ተከሳሹ ነፍሰ ገዳይ ነው፡፡ በእርግጥ ይገደል፡፡ 18 የተከሰሰው ሰው ተበዳዩን ሊገድል በሚችል የእንጨት መሳሪያ ቢመታውና ተበዳዩ ቢሞት ተከሳሹ በእርግጥ ነፍሰ ገዳይ ነው፡፡ ሊገደል ይገባዋል፡፡ 19 ደም ተበቃዩ ራሱ ነፍሰ ገዳዩን ይግደለው፡፡ ሲያገኘው፣ ሊገድለው ይችላል፡፡ 20 ተከሳሹ አንድን እየተደበቀ ወይም እየተሸሸገ ያለ ሰው በጥላቻ ቢገፈትረው ወይም አንዳች ነገር ቢወረውርበትና ከዚህም የተነሳ ተበዳዩ ቢሞት፣ 21 ወይም በጥላቻ መትቶ ቢጥለውና ከዚህም የተነሳ ተበዳዩ ቢሞት መትቶ የገደለው በእርግጥ ይገደል፡፡ ነብስ ገዳይ ነው፡፡ ደም ተበቃዩ ነብሰ ገዳዩን ሲያገኘው ይግደለው፡፡ 22 ነገር ግን ተከሳሹ ሰው ቀድሞ ባልታሰበበት ጥላቻ ተበዳዩን ቢመታው ወይም ሳያስበው አንዳች ነገር ወርውሮ ቢመታው፣ 23 ተበዳዩን ሳይመለከት ሊገድለው የሚችል ድንጋይ ቢወረውርበት፣ ተከሳሹ የተበዳዩ ጠላት አይደለም፤ ተበዳዩን ለመጉዳት እየሞከረ አልነበረም፡፡ የሆነ ሆኖ ተበዳዩ ቢሞት፣ 24 በዚህ ሁኔታ፣ ማህበረሰቡ በተከሳሹና በደም ተበቃዩ መሀል በእነዚህ ህጎች መሠረት ይዳኝ 25 ማህበረሰቡ ተከሳሹን ከደም ተበቃዩ እጅ ያድነው፡፡ ማህበረሰቡ ተከሳሹን በመጀመሪያ ወዳሸሸበት መሸሸጊያ ከተማ ይመልሰው፡፡ ተከሳሹ፣ በቅዱሱ ዘይት የተቀባው በወቅቱ ያለው ሊቀካህን እስኪሞት ድረስ በዚያ ይኑር፡፡ 26 ነገር ግን የተከሰሰው ሰው በማንኛውም ጊዜ ከሸሸበት ከተማ ድንበር አልፎ ቢሄድ፣ 27 እና ደም ተበቃዩ ከመሸሸጊያ ከተማው ድንበር ውጭ ቢያገኘውና ቢገድለው፣ ደም ተበቃዩ በነብሰ ገዳይነት ጥፋተኛ አይሆንም፡፡ 28 ለዚህም ምክንያቱ ተከሳሹ ሰው እስከ ሊቀ ካህኑ ሞት ድረስ በመሸሸጊያ ከተማው መቆየት ስለነበረበት ነው፡፡ 29 እነዚህ ህጎች፤ በምትኖባቸው ቦታዎች ሁሉ፣ በትውልዳቸው ሁሉ ለእናንተ የጸኑ ናቸው፡፡ 30 ሰውን የገደለ ማንኛውም ሰው፣ በምስክሮች ቃል እየረጋገጠ መገደል አለበት፡፡ ነገር ግን የአንድ ምስክር ቃል ብቻውን ማንንም ሰው ለመግደል በቂ አይደለም፡፡ 31 ደግሞም፣ በነብስ ገዳይነት ጥፋተኛ ለሆነ ሰው ሕይወት የነፍስ ዋጋ አትቀበሉ፡፡ ያ ሰው በእርግጥ ይገደል፡፡ 32 ወደ መሸሸጊያ ከተማ ለሄደ የነፍስ ዋጋ አትቀበሉ፡፡ ሊቀ ካህኑ እስኪሞት ድረስ የነፍስ ዋጋ በመቀበል ወደ ራሱ ርስት ተመልሶ እንዲገባ አትፍቀዱለት፡፡ 33 በዚህ መንገድ የምትኖሩባትን ምድር አታርክሱ፣ ምክንቱም በነፍስ ግድያ የሚፈስ ደም ምድሪቱን ያረክሳል፡፡ ምድር በላይዋ ደም ሲፈስ፣ ደም ካፈሰሰው ሰው ደም በስተቀር ሌላ ምንም ማስተስረያ ማድረግ አይቻልም፡፡ 34 ስለዚህ የምትኖሩባትን ምድር አታርክሱ ምክንያቱም እኔ በውስጧ እኖራለሁ፡፡ እኔ፣ ያህዌ፣ በእስራኤል ሰዎች መሃል እኖራለሁ፡፡”



Numbers 35:1

ሜዳ

ሠፊ ሆኖ ለጥ ያለ ሜዳ

ለሌዋውያን የሚደርሳቸውን የመሬት ድርሻ ስጧቸው

እግዚአብሔር የራሣቸው የሆነ መሬትለሌዋውያንያልሰጣቸው በመሆኑ በሌሎች ነገዶች ከተማዎች ውስጥ መቀመጥ ነበረባቸው፡፡

የግጦሽ መሬት

እንስሳት ሣር የሚግጡባቸው የመሬት ክፍል

Numbers 35:3

አንድ ሺህ ክንድ

“1000 ክንድ”ዘመናዊ የርቀት መለኪያን መጠቀም ከፈለጋችሁ ከዚህ በሚከተለው መልኩ ለማድረግ ትችላላችሁ፡፡“457 ሜትር”(ቁጥሮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ርቀት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:5

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሰዎች ምን ማድረግ እንደሚገባቸው ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ሁለት ሺህ ክንድ

“2000 ክንድ”አንድ ክንድ 46 ሴንቲ ሜትር ነው፡፡(ቁጥሮችና መፅሐፍ ቅዱሣዊ ርቀት የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:6

የሰው ነፍስ ያጠፋ ሰው

ይሄ የሚያመለክተው የሰው ነፍስ ያጠፉ ሰዎችን ሲሆን ነገር ግን ሰውዬውን የገደሉት ሆን ብለው ነው ወይስ ሳያስቡት ነው? የሚለውጥያቄ ግን ገና ውሳኔ ያላገኘ መሆኑን ነው፡፡

አርባ ሁለት…አርባ ስምንት

“42...48” (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:8

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሰዎች ምን ማድረግ እንደሚገባቸው ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

Numbers 35:9

በስህተት

በድንገት ወይም ሳያደፍጡ ወይም ሆን ብለው ሳይጠብቁ

Numbers 35:12

ደም ተበቃይ

ጥፋተኛ የሆነውነ ሰው ለመበቀል የሚያደባ የቅርብ ዘመድን ነው፡፡

በማህበሩ ፊት ለፊት እስኪቆም ድረስ እንዳይሞት

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ጥፋተኛው ሰው ወደ ማህበሩ ፈርዶ ፍርዱን ለማግኘቱ በፊት አንድ ሰው እንዳይገድለው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:14

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሰዎች ምን ማድረግ እንደሚገባቸው ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

Numbers 35:16

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሰዎች ምን ማድረግ እንደሚገባቸው ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ፈፅሞ ይገደል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በእርግጥም ልትገድሉት ይገባል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውንና ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:19

ደም ተበቃዩ

እዚህ ላይ“ደም”የሚለው ቃል መግደል ለሚለው ሃሣብ ሌላ ገላጭ ቃል ነው፡፡“የገደለውን ሰው የሚበቀል” ወይም “ለመበቀል የሚፈልግ የቅርብ ዘመድ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ደም ተበቃዩ ባገኘው ጊዜ ነፍሰ ገዳዩን ይግደለው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የቅርብ ዘመድ የሆነ ሰው ጥፋተኛውን ሰው መግደል አለበት“ ወይም “ጥፋተኛው ሰው መሞት አለበት”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:22

ጥላቻ ሳይኖረው በድንገት

“ከጥላቻ የተነሣ ቀደም ሲል ጉዳዩን በተመለከተ ላይ ዕቅድ ሳይነድፍ”

ሳይሸምቅ

አንድ ሰው ሌላን ሰው ሆነ ብሎ ለመጉዳት የሚያደርገው ክትትል አንድ ሰው ለማጥቃት ደፈጣ የሚያደርግ አስመስሎ ነው የተገለፀው፡፡“የሚጠቃውን ሰው ለመጉዳትት ሆነ ተብሎ ያልተደረገ” (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:24

ደም ተበቃዩ

እዚህ ላይ“ደም”የሚለው ቃል መግደል ለሚለው ሃሣብ ሌላ ገላጭ ቃል ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 35፡19 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

ማህበሩም ነፍሰ ገዳዩን ሰው ከደም ተበቃዩ እጅ ያድነዋል

ይሄ ማለት ማህበሩ ግድያው የተፈፀመው በአጋጣሚ ነው ብሎ የሚያስብ ከሆነ የተገደለው ሰው የቅርብ ዘመድ የሆነ ሰው እንዳይገድለው ያድኑታል፡፡ነገር ግን ማህበሩ ግድያው የተፈፀመው ታስቦበት እንደሆነ ካመነ የሟች የቅርብ ዘመድ የሆነ ሰው ጥፋተኛውን ሰው መግደል ይኖርበታል፡፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በቅዱስ ዘይትም የተቀባው

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በቅዱስ ዘይት የቀባኸው ሰው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:26

ደም ተበቃዩ

እዚህ ላይ“ደም”የሚለው ቃል መግደል ለሚለው ሃሣብ ሌላ ገላጭ ቃል ነው፡፡ይህንን ሐረግ በዘኁልቁ 35፡19 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 35:29

አጠቃላይ መረጃ

እግዚአብሔር ሰዎች ምን ማድረግ እንደሚገባቸው ለሙሴ መናገሩን ይቀጥላል፡፡

ለልጅ ልጃችሁ

“ከአንተ በኋላ ለሚመጡት ትውልዶቹ በሙሉ”

Numbers 35:31

እርሱ ፈፅሞ ይገድል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እርሱን ልትገድሉት ይገባቸኋል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውንና ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በራሱ ንብረት ላይ እንዲቀመጥ አትፍቀዱለት

ይሄ የሚያመለክተው የመማፀኛ ከተማውን ለቅቆ ወደ ቤቱ ለመመለስ የፈለገን ሰው ነው፡፡“የመማፀኛ ከተማውን ለቅቆ እንዲሄድ መደፍቀድ የለባችሁም፡፡ወደ ቤቱ በመሄድ በራሱ ንብረት ላይ እንዲቀመጥ መፍቀድም የለባችሁም፡፡”(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በዚህ ሁኔታ

“የነፍስ ዋጋን በመቀበል”

Numbers 35:33

የምትኖሩባትን ምድር አታርክሷት፤በደም አፍሳሹ ደም ካልሆነ በቀር ምድሪቱ ከፈሰሰባት ደም አትነፃም

በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት የሌለው ምድር አካሉ እንደተመረዘ ነገር ተገልጿል፡፡ከሰው መግደል ጋር በተያያዘ የፈሰሰው ደም ምድሪቱ በእኔ ዘንድ ተቀባይነት እንዳይኖራት የሚያደርግ በመሆኑ በዚህ ዓይነትሁኔታ ምድራችሁ በፊቴ ተቀባይነት እንዳይኖራት አታድርጉ፡፡(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በዚህ ሁኔታ

“የነፍስ ዋጋን በመቀበል”

በደም አፍሳሹ ደም ካልሆነ በቀር ምድሪቱ ከፈሰሰባት ደም አትነፃም

ይሄ የሚያመለክተው አንድ ሰው ሆነ ብሎ ሌላ ሰው የገደለ ሲሆን ነው፡፡“አንድ ሰው በምድሪቱ ላይ ደም የሚያፈስስ ከሆነ ምድሪቱ የምትነፃው ያ ደም ያፈሰሰው ሰው ሲገደል ብቻ ነው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 36

1 ከዚያ ከዮሴፍ ትውልዶች ጎሣ የሆኑት፣ የአባቶቻቸው ቤተሰቦች መሪዎች፣ የምናሴ ልጅ በሆነው በሚኪር ልጅ ገለዓድ የተመሠረተው ጎሳ በሙሴና በእስራኤላዊያን አባቶች ቤተሰቦች አለቆች ፊት መጥተው ተናገሩ፡፡ 2 እንዲህም አሉ፣ “ጌታችን ሆይ፣ ያህዌ ለእስራኤል ህዝብ ርስታቸውን በዕጣ እንድታካፍላቸው አዞሃል፡፡ የወንድማችንን የሰለጰዓድን ድርሻ ለሴት ልጆቹ እንድትሰጥ ያህዌ አዝዞህ ነበር፡፡ 3 ነገር ግን ሴት ልጆቹ ከእስራኤል ሰዎች ከሌላ ጎሣ ወንዶችን ቢያገቡ፣ ድርሻቸው የሆነው መሬት ከአባቶቻችን ድርሻ ተነቅሎ ወደ ሌላ ጎሣ ይተላለፋል፡፡ መሬቱ የገቡበት የሌላ ጎሳ ድርሻ ይሆናል፡፡ በዚያ ሁኔታ፣ ከእኛ ርስትነት ይነቀላል፡፡ 4 ይህ ሲሆን፣ የእስራኤል ኢዮቤልዩ ሲመጣ፣ የእነርሱ ድርሻ የተጋቧቸው ጎሣዎች ርስት ይሆናል፡፡ በዚህ መንገድ የእነርሱ ድርሻ ከእኛ አባቶች ጎሣ ይወሰዳል፡፡ 5 ስለዚህም ሙሴ በያህዌ ቃል ለእስራኤል ሰዎች ትዕዛዝ ሰጠ፡፡ እንዲህም አለ፣ “የዮሴፍ ትውልዶች ጎሣ የተናገሩት ትክክል ነው፡፡ 6 ያህዌ ስለ ሰለጰዓድ፣ ሴት ልጆች ያዘዘው ይህ ነው፡፡ እንዲህም አለ፣ ‘የመረጡትን ያግቡ፣ ነገር ግን ማግባት ያለባቸው ከአባታቸው ጎሣ ብቻ ነው፡፡’ 7 የእስራኤል ሰዎች ድርሻ ከአንድ ጎሣ ወደ ሌላው መሄድ የለበትም፡፡ እያንዳንዱ እስራኤላዊ የራሱን ጎሣ ድርሻ ይዞ መቀጠል አለበት፡፡ 8 ከጎሣዋ ርስት የወረሰች እያንዳንዷ የእስራኤል ሴት፣ ማግባት ያለባት ከአባቷ ጎሣ ውስጥ ብቻ ነው፡፡ ይህ የሚሆነው እያንዳንዱ እስራኤላዊ የአባቶቹን ርስት ይዞ እንዲኖር ነው፡፡ 9 ከአንዱ ጎሣ ወደ ሌላው ምንም ርስት መተላለፍ የለበትም፡፡ የእስራኤል ህዝብ እያንዳንዱ ጎሣ የራሱን ርስት ይዞ መቀጠል አለበት፡፡” 10 ስለዚሀ የሰለጰዓድ ሴት ልጆች ያህዌ ሙሴን እንዳዘዘው አደረጉ፡፡ 11 የሰለጰዓድ ሴት ልጆች ማህለህ፣ ቲርጳ፣ ጌግላ፣ ሚልካ፣ ኑዔ 12 ልጅ የምናሴትን ትውልዶች አገቡ፡፡ በዚህ መንገድ፣ ርስታቸው የአባታቸው ጎሣ ርስት ሆኖ ቀረ፡፡ 13 ያህዌ በሙሴ በኩል በሞአብ ሜዳዎች በዮርዳኖስ ኢያሪካ ላይ ለእስራኤል ሰዎች የሰጣቸው ትዕዛዛትና ድንጋጌዎች እነዚህ ናቸው፡፡



Numbers 36:1

ማኪር

ይሄ የሰው ሥም ነው፡፡የዚህን ሰው ሥም በዘኁልቁ 26፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

በእግዚአብሔር ታዝዘሃልና

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“እግዚአብሔር አዝዞሃል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰለጰዓድ

ይሄ የሰው ሥም ነው፡፡የዚህን ሰው ሥም በዘኁልቁ 26፡33 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 36:3

ከአባቶቻችን ነገድ ርስት ይጎድላል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“በአባቶቻችን ርስት ውስጥ ድርሻ አይኖረውም”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ይጨመራል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ድርሻው የሚሆነው…”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ከአባቶቻችን ርስት ይነቀላል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የርስታችን አካል አይሆንም”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእሥራኤልም ልጆች ኢዩቤልዩ

ይሄ የሚያመለክተው በየሃምሣ ዓመቱ የሚደረገውን በዓል ነው፡፡በዚህ የበዓል ወቅት አንድ ሰው የሸጠው መሬትም ሆነ ንግድ ወደ መጀመሪያ ባለቤቱ መመለስ ይኖርበታል፡፡(በግምት ላይ የተመሠረተ ዕውቀትና የተሟላ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ድርሻቸው ይጨመራል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ድርሻቸው ….”

ርስታቸው ከአባቶቻችን ነገድ ርሰት ይጎድላል

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የእኛን ነገድ የመሬት ድርሻ ይወስዱታል”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 36:5

እንደ እግዚአብሔር ቃል

“እግዚአብሔር በተናገረው መሠረት”

የወደዱትን ያግቡ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“ደስ ያላቸውን ሰው ያግቡ”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

ነገር ግን ከአባታቸው ነገድ ብቻ ያግቡ

ይሄ በድርጊት መልክ ሊገለፅ ይችላል፡፡“የሚያገቡትን ሰው ግን ከአባታቸው ቤት ብቻ ነው ማግባት የሚኖርባቸው”(ገቢራዊ ወይም ፍዝ የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 36:7

ድርሻ አይኖርም

“ድርሻ”የሚለው ቃል የሚያመለክተው እንዳንዱ ነገድ በርስት መልክ የሚቀበለውን መሬት ነው፡፡“ምንም ዓይነት የመሬት ድርሻ”(ከዋናው ሃሣብ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመግለፅ የሚውል ቃል የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 36:8

በአባቷ ቤት ርስት ያላት

“በነገዷ ውስጥ የመሬት ርስት ያላት”

ርስትንሊቀበል ይችላል

እያንዳንዱ ነገድ ንብረቱ የሚያደርገውን መሬት እንደሚቀበሉት ዓይነት ውርስ ተደርጎ ነው የሚነገረው፡፡ (ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከአንድ ነገድ ወደ ሌላ ነገድ ምንም ርስት አይተላለለፍ

ባለቤትነትን ከአንድ ነገድ ወደ ሌላ ማስተላለፍን በተመለከተ ልክ አንድ ንብረት ከአንድ ሰው እጅ ወደ ሌላ ሰው እጅ እንደተላለፈ ዓይነት ተደርጎ ነው የሚገለፀው፡፡“ማንም ሰው ቢሆን የመሬት ድርሻ ባለቤትነትን ከአንድ ነገድ ወደ ሌላ ነገድ ማስተላለፍ አይኖርበትም”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 36:10

ማህለህ፤ቲርጳ፤ኤግላ፤ሚልካ፤ኑዓ

እነዚህን ስሞችበዘኁልቁ 26፡33 ላይ እንዴት እንደተረጎማችሁት ተመልከቱ፡፡(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ይመልከቱ)

ርስታቸው

የሰለጰዓድ ሴቶች ልጆች በንብረትነት የወሰዱት መሬት ልክ እንደወረሱት ውርስ ተደርጎ ተገልጿል፡፡“በውርስ መልክ የተቀበሉት መሬት”(ምሣሌያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Numbers 36:13

ሜዳዎች

ሰፊና ለጥ ያለ መሬት


Book: Deuteronomy


Deuteronomy

Chapter 1

1 ሙሴ በዮርዳኖስ ማዶ በምድር በዳ በዮርዳኖስ ወንዝ ሸለቆ ሜዳ በዓረባ፥ በፋራን፥ በጦፌል፥ በላባን፥ በሐጼሮት፥ በዲዛሃብ መካከል ሳሉ፥ ለአስራኤል ሁሉ የተናገራቸው እነዚህ ቃላት ናቸው። 2 በሴይር ተራራ መንገድ ከኮሬብ እስከ ቃዴስ በርኔ ድረስ የአሥራ አንድ ቀን ጉዞ ነው። 3 በአርባኛው ዓመት በአሥራ አንደኛው ወር ከወሩም በመጀመሪያው ቀን ሙሴ እግዚአብሔር ስለ እነርሱ ያዘዘውውን ሁሉ ለእስራኤል ሕዝብ ነገራቸው። 4 ይህም እግዚአብሔር በሐሴቦን ይኖር የነበረውን የአሞራውያንን ንጉሥ ሴዎንን፥ በአስታዎትና በኤድራይ ይኖር የነበረውንም የባሳንን ንጉሥ ዐግን ከመታ በኋላ ነበር። 5 በዮርዳኖስ ማዶ በሞዓብ ምድር ሙሴ እንዲህ ብሎ እነዚህን መመሪያዎች ይናገር ጀመር፦ 6 እግዚአብሔር አምላካችን በኮሬብ እንዲህ ብሎ ተናገረን፦ በዚህ ተራራ የኖራችሁበት ይብቃችሁ። 7 ጉዞኣችሁን ወደ ኮረብታማው ወደ አሞራውያን አገር ወደ ድንበሮቹም፥ ሁሉ በዓረባም በደጋውና በቆላው፥ በደቡብና በባሕር ዳር ወዳሉ ወደ ከነዓናውያን ምድር፥ ወደ ሊባኖስ ወንዝ ሸለቆ እስከ ታላቁ ኤፍራጥስ ወንዝ ድረስ ሄዱ። 8 እነሆ ምድሪቱን በፊታችሁ አድርጌአለሁ፤ እግዚአብሔር ለአባቶቻችሁ ለአብርሃም፥ ለይስሐቅና ለያዕቆብ፥ ከእነርሱም በኋላ ለዘራቸው ይሰጣቸው ዘንድ የማለላቸውን ምድር ሂዱና ውረሱ። 9 በዚያን ጊዜ እንዲህ ብዬ ተናግሬአችሁ ነበር፦ እኔ በራሴ ብቻዬን ልሸከማችሁ አልችልም። 10 እግዚአብሔር አምላካችሁ አብዝቶአችኋል፥ እነሆም እናንተ ዛሬ እንደ ሰማይ ከዋክብት ብዙ ናችሁ። 11 የአባቶቻችሁ እግዚአብሔር አምላክ ሺህ ጊዜ ሺህ ያድርጋችሁ፤ ተስፋ እንደሰጣችሁም ይባርካችሁ። 12 ነገር ግን እኔ በራሴ ድካማችሁን፥ ሸክማችሁንና ክርክራችሁን እሸከም ዘንድ ብቻዬን እንዴት እችላለሁ? 13 ከእናንተ መካከል ከየነገዶቻችሁ ጥበበኞች፥ አስተዋዮችና አዋቂዎች የሆኑትን ሰዎች ምረጡ፤ እኔም እነርሱን የእናንተ አለቆች አደርጋቸዋለሁ ብዬኣችሁ ነበረ። 14 እናንተም እንዲህ ብላችሁ መለሳችሁ፦ የተናገርከንን ነገር ለማድረግ ለእኛ መልካም ነው። 15 ስለዚህም ጥበበኞችና አዋቂዎች የሆኑትን የነገዶቻችሁን ወሰድሁ፥ በእናንተም ላይ አለቆች እንዲሆኑ የሺህ አለቆች፥ የመቶ አለቆች፥ የአምሳ አለቆች፥ የአሥር አለቆችና ሹማምንት በየገዶቻችሁ አደረግኋቸው። 16 በዚያን ጊዜም ፈራጆቻችሁን እንዲህ ብዬ አዘዝኳቸው፦ በወንድሞቻችሁ መካከል፤ በሰውና በወንድሙ መካከልና በመጻተኛ ላይ በጽድቅ ፍረዱ። 17 በክርክርም ጊዜ ለማንም ፊት አድልዎ አታድርጉ፥ ታላቁን እንደምትሰሙ፥ ታናሹንም ስሙ። ፍርድ የእግዚአብሔር ስለሆነ የሰው ፊት መፍራት አይገባችሁም። ከክርክርም አንድ ስንኳ ቢከብዳችሁ ወደ እኔ አምጡት እኔም እሰማዋለሁ። 18 በዚያን ጊዜም ልታደርጉት የሚገባችሁን ነገር ሁሉ አዘዝኋችሁ። 19 ከኮሬብም ተነስተን፥እግዚአብሔር አምላካችን እንዳዘዘን እንዳያችሁትም በታላቁና እጅግ አስቸጋሪ በሆነ ምድረ በዳ ሁሉ ተጉዘን በተራራማው በአሞራውን አገር ሄድን፥ ወደ ቃዴስ በርኔም መጣን። 20 እኔም እንዲህ አልኋችሁ፦ እግዚአብሔር አምላካችን ወደ ሚሰጠን ወደ ተራራማው አሞራውያን አገር መጣችኋል። 21 እነሆ እግዚአብሔር አምላካችሁ ምድሪቱን በፊታችሁ አድርጎአል፤ የአባቶቻችሁ አምላክ እግዚአብሔር እንዳላችሁ ውጡ፥ ውረሱአት፥ አትፍሩ አትደንግጡም። 22 ከእናንተም ሁላችሁ ወደ እኔ መጥታችሁ እንዲህ አላችሁ፦ ምድሪቱን እንዲሰልሉልንና እናጠቃቸው ዘንድ የሚገባንን የመንገዱንና የምንገባባቸውን ከተሞች ሁኔታ ተመልሰው እንዲነግሩን ከፊታችን ሰዎችን እንድስደድ። 23 ነገሩም ደስ አሰኘኝ፤ ከእናንተም ከየነገዱ ሁሉ አንድ አንድ ሰው፥ አሥራ ሁለት ሰዎችን መረጥሁ። 24 እነርሱም ወደ ተራራማው አገር ሄዱ፥ ወደ ኤሽኮልም ሸለቆ መጥተው ሰለሉአት። 25 እነርሱም ከምድሪቱ ፍሬ በእጃቸው ወሰዱ፥ ወደ እኛም ይዘውት መጡ። እነርሱም ደግሞ፦ እግዚአብሔር አምላካችን የሚሰጠን ምድር መልካም ናት ብለውም አወሩልን። 26 ምድሪቷንም ማጥቃት እንቢ ብላችሁ፥ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ላይ ዐመፃችሁ፥ ። 27 በድንኳናችሁም ውስጥ እንዲህ እያላችሁ አጉረመረማችሁ፦ እግዚአብሔር ስለ ጠላን እንዲያጠፋን በአሞራውያን እጅ አሳልፎ ይሰጠን ዘንድ ከግብፅ ምድር አወጣን። 28 አሁን ወዴት መሄድ እንችላለን? ሕዝቡ ብዙ ነው፥ ቁመቱም ከእኛ ይረዝማል ከተሞቹም ታላላቆች፥ የተመሽጉና እስከ ሰማይም የደረሱ ናችው፥ የዔናቅንም ልጆች ደግሞ በዚያ አየናቸው፤ ብለው ወንድሞቻችን ልባችንን እንዲቀልጥ አደረጉ። 29 እኔም አልኋችሁ፦ አትደንግጡ፥ እነርሱንም አትፍሩአቸው። 30 በፊታችሁ የሚሄደው እግዚአብሔር አምላካችሁ ስለ እናንተ ይዋጋል፥ በፊታችሁም በግብፅና በምድረ በዳ እንዳደረገላችሁ ሁሉ፤ 31 ወደዚህም ስፍራ እስክትመጡ ድረስ በሄድዳችሁበት መንገድ ሁሉ ሰው ልጁን እንደሚሸከም እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ተሸከማችሁ እናንተ አይታችኋል። 32 ዳሩ ግን እግዚአብሔር አምላካችሁን በዚህ ነገር አላመናችሁትም፤ 33 በፊታችሁም ሆኖ በምትሄዱበት መንገድ ድንኳናችሁን እንድታቆሙ ቦታ እንድታገኙና በሌሊት በእሳት፥ በቀንም በደመና እንድትሄዱ መንገዱን ያሳታችሁ እርሱ ነው። 34 እግዚአብሔርም የቃላችሁን ድምፅ ሰምቶ ተቆጣ፥ ምሎም፥ እንዲህ አለ፦ 35 በርግጥ ለአባቶቻችሁ እሰጣቸው ዘንድ የማልሁላቸውን መልካሚቱን ምድር ከዮፎኒ ልጅ ከካሌብ በቀር ከእነዚህ ሰዎች ከዚህ ክፉ ትውልድ ማንም አያይም። 36 እርሱም እግዚአብህሔርን ፈጽሞ ተከትሎአልና የረገጣትን ምድር ለእርሱና ለልጆቹ እሰጣለሁ ብሎ ማለ። 37 እግዚአብሔርም ደግሞ በእናንተ ምክንያት እኔን ተቆጣኝ እንዲህም አለ፦ አንተ ደግሞ ወደዚያ አትገባም 38 በፊትህ የሚሄድ አገልጋይ የነዌ ልጅ ኢያሱ ወደዚያ ይገባል፥ እርሱም እስራኤላውያን ምድሪቱን እንዲወርሱ ይመራቸዋልና፤ አደፋፍረው። 39 ከዚህም በተጨማሪ፦ ለጉዳት ይዳረጋሉ፥ ዛሬም መልካሙንና ክፉውን መለየት የማይችሉ ናቸው ያላችኋችሁ ታናናሽ ሕፃናታችሁ ልጆቻችሁ እነርሱ ወደዚያ ይገባሉ። ምድሪቱንም ለእነርሱ እሰጣለሁ ይወርሱታልም። 40 እናንተ ግን ተመልሳችሁ በኤርትራ ባሕር መንገድ ወደ ምድረ በዳ ሂዱ። 41 እናንተም፦ እግዚአብሔርን በድለናል፥ እግዚአብሔር አምላክችሁ እንዳዘዘን ሁሉ እንወጣለን፥ እንዋጋማለን ብላችሁ መለሳችሁልኝ። ከእናንተም ሰው ሁሉ የጦር መሣሪያውን ያዘ፥ ወደ ተራራማውም አገር ለመውጣትና ለማጥቃት ተዘጋጀ። 42 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ እኔ በእናንተ መካከል ስለማልገኝ፥ በጠላቶቻችሁ ፊት እንዳትሸነፉ አትውጡ፥ አትዋጉም በላቸው አለኝ። 43 እኔም ተናገርኋችሁ እናንተም አልሰማችሁም። በእግዚአብሔር ትእዛዝ ላይ ዐመፃችሁ፥ አልሰማችሁም በትዕቢታችሁም ወደ ተራራማው አገር ለማጥቃት ወጣችሁ። 44 ነገር ግን በተራራማው አገር ይኖሩ የነበሩ አሞራውያን በእናንተ ላይ ወጥተው እንደ ንብ አሳደዱአችሁ፥ እስከ ሔርማም ድረስ በሴይር መቱአችሁ። 45 ተመልሳችሁም በእግዚአብሔር ፊት አለቀሳችሁ፤ እግዚአብሔር ግን ድምፃችሁን አልሰማም፥ ወደ እናንተም አላዳመጠም። 46 ሁሉም ቀናት በቆያችሁባችሁ ለብዙ ቀን በቃዴስ ተቀመጣችሁ።



Deuteronomy 1:1

ከዮርዳኖስ ማዶ

ይህ የሚያመለክተው ከእስራኤል በስተምስራቅ የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግሮ ያለውን ምድር ነው። ሙሴ ለእስራኤላውያን በሚናገርበት ጊዜ ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ ነበር። አ.ት፡ ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ

ሱፋ … ፋራን … ቶፌል … ላባ … ሐጼሮት … ዘሀብ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከኮሬብ እስከ ቃዴስ በርኔ የአሥራ አንድ ቀን መንገድ ነው

“ከኮሬብ ወደ ቃዴስ በርኔ ለመጓዝ አሥራ አንድ ቀን ይፈጃል”

የሴይር ተራራ

ይህ ከሙት ባህር በስተደቡብ ያለ ተራራማ አካባቢ ነው። አካባቢው “ኤዶም” በመባልም ይታወቃል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አሥራ አንድ

“11” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 1:3

ሙሴ በአርባኛው ዓመት፣ በአሥራ አንደኛው ወር፣ ከወሩም በመጀመሪያው ቀን ተናገረ

መቁጠሪያ ቁጥሮች ወደ ተራ ቁጥሮች ሊተረጎሙ ይችላሉ። አ.ት፡ “ሙሴ በተናገራቸው ጊዜ በምድረ በዳ የኖሩት ለ40 ዓመታት፣ ለ11 ወራትና ለ1 ቀን ነበር። (መቁጠሪያ ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አርባኛ

40ኛ (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በአሥራ አንደኛው ወር፣ ከወሩም በመጀመሪያው ቀን

ይህ በዕብራውያኑ የቀን አቆጣጠር አሥራ አንደኛው ወር ነው። የመጀመሪያው ቀን በምዕራባውያን አቆጣጠር ወደ ጥር ወር አጋማሽ ይቃረባል።(የዕብራውያን ወራት እና መቁጠሪያ ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አሥራ አንደኛ

11ኛ (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ያህዌ

ይህ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ራሱን ለሕዝቡ የገለጠበት ስሙ ነው። ያህዌ እንዴት እንደሚተረጎም ለመረዳት የትርጉም ቃል ገጽን ተመልከት።

እግዚአብሔር ወግቷቸው ነበር

“እስራኤላውያን እንዲያሸንፉ እግዚአብሔር አስችሏቸው ነበር”

ሴዎን … ዐግ

እነዚህ የነገሥታት ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሐሴቦን … አስታሮትን በኤድራይ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 1:5

ከዮርዳኖስ በላይ

ይህ የሚያመለክተው ከእስራኤል በስተምስራቅ ከዮርዳኖስ ወንዝ ባሻገር ያለውን ምድር ነው። ሙሴ ይህንን በሚናገርበት ጊዜ ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ ነበር። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 1፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ”።

ለእኛ ተናገረን

“እኛ” የሚለው ቃል ሙሴንና ሌላውን የእስራኤል ሕዝብ ያመለክታል።

በዚህ ኮረብታማ አገር ብዙ ዓመት ኖራችኋል

ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ከዚህ በኋላ በዚህ ተራራ አጠገብ መቆየት አይኖርባችሁም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 1:7

ተመልሳችሁ ጉዞአችሁን ቀጥሉ

“ተመልሳችሁ” የሚለው ቃል አንድን ተግባር ለመጀመር ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “እንደገና ጉዞአችሁን ቀጥሉ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ኮረብታማ አገር -- ኤፍራጥስ

እግዚአብሔ ለእስራኤላውያን ለመስጠት ቃል በገባላቸው ምድር አካባቢዎቹን እያብራራላቸው ነው።

ኮረብታማ አገር

ይህ አሞራውያን ይኖሩ ከነበሩበት አቅራቢያ የሚገኝ ኮረብታማ አካባቢ ነው።

ቆላ

ዝቅና ለጥ ያለ የምድር አካባቢ

ተመልከት

“ለምናገረው ነገር ትኩረት ስጡ”

ምድሪቱን በፊታችሁ አስቀምጫለሁ

“አሁን ይህችን ምድር ሰጥቻችኋለሁ”

እግዚአብሔር የማለላችሁን ያንን

እግዚአብሔር ራሱን እንደ ሌላ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “እኔ እግዚአብሔር ምያለሁ” (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

አባቶች

“አባቶች” የሚለው ቃል አያት፣ ቅድም አያቶችን ሁሉ የሚወክል ነው። አ.ት፡ “አያት፣ ቅድም አያቶች” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 1:9

በዚያን ጊዜ ነገርኳችሁ

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው ሙሴን ነው። “በዚያን ጊዜ” የሚለው ሐረግ እስራኤላውያን በኮሬብ፣ ይኸውም የሲና ተራራ ራሱ ነው፣ በዚያ የነበሩበትን ጊዜ ነው። አ.ት፡ “በኮሬብ በነበርንበት ጊዜ ነገርኳችሁ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ለብቻዬ ልሸከማችሁ አልችልም

እዚህ ጋ “ልሸከማችሁ” ማለት “ልመራችሁ” ወይም “ላስተዳድራችሁ” ማለት ነው። አ.ት፡ “በራሴ ልመራችሁ ይከብደኛል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛውን

ይህ ግነት ሲሆን ትርጉሙም እግዚአብሔር የእስራኤላውያንን ቁጥር እጅግ አብዝቶታል ማለት ነው። አ.ት፡ “እጅግ ብዙ ሕዝብ”(ግነት፣ ጥቅል አስተያየት እና Simile)

አንድ ሺህ ጊዜ

“አንድ ሺህ” የሚለው ሐረግ “በጣም ብዙ” የሚል ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “በጣም ብዙ ጊዜ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አንድ ሺህ

1000 (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 1:12

ይሁን እንጂ፣ ችግራችሁን፣ ሸክማችሁንና ክርክራችሁን ለብቻዬ እንዴት መሸከም እችላለሁ?

ሙሴ ችግሮቻቸውን በሙሉ ለብቻው መፍታት እንደማይችል አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ይጠይቃል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ችግራችሁን፣ ሸክማችሁንና ክርክሮቻችሁን ለብቻዬ መሸከም አልችልም”። (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ችግራችሁን፣ ሸክማችሁን

ሙሴ የተሸከመውና ሊፈታቸው ያስፈልጉ የነበሩት የሕዝቡ ችግሮችና ቅሬታዎች ለእርሱ ልክ ቁስ አካል የመሸከም ያህል እንደከበዱት ይናገራል። አ.ት፡ “ችግሮቻችሁን፣ ቅሬታዎቻችሁን መፍታት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ክርክራችሁን

“ሙግታችሁን” ወይም “አለመግባባቶቻችሁን”

ከየነገዱ መልካም ስም ያላቸውን ሰዎች

“ከእያንዳንዱ ነገድ እስራኤላውያን የሚያከብሯቸው ሰዎች”

Deuteronomy 1:15

መልካም ስም ያላቸውን ሰዎች

“ወገኖቻችሁ የሚያከብሯችሁን ሰዎች”። ይህ በዘዳግም 1፡13 ላይ እንዴት እንደተተረጎመ ተመልከት።

የሺዎች _ የመቶዎች _ የሃምሳዎች _ የአሥሮች

የ1000 ቡድን _ የ100 ቡድን _ የ50 ቡድን _ እና የ10 ቡድን (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሻምበሎች _ መኮንኖች

እነዚህ በእስራኤል መንግሥት የተለያዩ መሪዎች የሚጠሩባቸው መጠሪያዎች ናቸው።

ነገድ በነገድ

“ከእያንዳንዳችሁ ነገድ”

በአንድ ሰውና በወንድሙ መካከል በጽድቅ ፍረዱ

“እስራኤላውያን እርስ በእርሳቸው በሚኖራቸው ክርክር ላይ ትክክለኛና ፍትሐዊ ውሳኔ ስጡ”

Deuteronomy 1:17

አድልዎ አታድርጉም

“አድልዎ አታድርጉ”

የታናሹንና የታላቁን እኩል ስሙ

“ታናሽ” እና “ታላቅ” የተባሉት እነዚህ ሁለት ጽንፎች ሕዝቡን ሁሉ ይወክላሉ። አ.ት፡ “ሕዝቡን ሁሉ በእኩል ትዳኙታላችሁ” (See: Merism)

የሰውን ፊት አትፈሩም

“ፊት” የሚለው ቃል የሰውን ሁለንተና የሚወክል ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። “አትፈሩም” ትዕዛዝ ነው። “ማንንም አትፍሩ” (See: Synecdoche)

በዚያን ጊዜ

ይህ ማለት በኮሬብ፣ በሲና ተራራ በነበሩበት ጊዜ ማለት ነው። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 1:19

ባያችሁት አስቸጋሪ ምድረ በዳ

“ያቋረጣችሁት ያ ሰፊና አደገኛ ምድረ በዳ

Deuteronomy 1:20

ተመልከቱ _ አምላካችሁ _ በፊታችሁ፤ ተነሡ፣ ውረሱ _ አባቶቻችሁ _ ለእናንተ፤ አትፍሩ፣ ተስፋም አትቁረጡ

ሙሴ ለአንድ ሰው የሚናገር ይመስል የሚናገረው ለእስራኤላውያን ነው፤ በመሆኑም እነዚህ ቅርጾች ብዙ ሳይሆኑ ነጠላ ቁጥር ናቸው። (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

ምድሪቱን በፊታችሁ አድርጓል

“አሁን ይህቺን ምድር ሊሰጣችሁ ነው”። ይህ በዘዳግም 1፡8 ላይ እንዴት እንደ ተተረጎመ ተመልከት

Deuteronomy 1:22

አሥራ ሁለት ሰዎች

“12 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ተመልሰው ሄዱ

መመለስ መመሪያውን ለመታዘዝ መጀመራቸውን የሚገልጽ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ያንን ስፍራ ትተው ሄዱ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የኤሽኮል ሸለቆ

ይህ ከኢየሩሳሌም በስተደቡብ የሚገን በኬብሮን አውራጃ የሚገኝ ሸለቆ ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ቃኙ

“መውጋት የሚችሉባቸውን አካባቢዎች ተመለከቱ”

Deuteronomy 1:25

ወሰዱ

“12ቱ ሰዎች ወሰዱ”

ከምድሪቱ ፍሬ ጥቂቱን በእጆቻቸው ወሰዱ

“ከምድሪቱ ፍሬ ጥቂቱን አነሡ”

ቃል አመጡልን፣ እንዲህም አሉን

ተናጋሪው “ቃል” አንድ ሰው ሊያመጣው የሚችለው ቁስ አካላዊ ነገር ይመስል ይናገራል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

‘አምላካችን እግዚአብሔር የሚሰጠን ምድር ጥሩ ነው’ አሉ

ቀጥተኛው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ተደርጎ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር አምላካችን የሚሰጠን ምድር ጥሩ እንደሆነ ተነግሯል”

Deuteronomy 1:26

እናንተ ግን ለመዋጋት እምቢ አላችሁ

እስራኤላውያን አሞራውያንን እንዲወጉና እንዲያጠፏቸው እግዚአብሔር አዘዛቸው፣ ነገር ግን እስራኤላውያን ፈሩ፣ ከእነርሱ ጋር ለመዋጋትም እምቢ አሉ”። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

በአሞራውያን እጅ

እዚህ ጋ “በ እጅ” ማለት ለአሞራውያን በእነርሱ ላይ የበላይ እንዲሆኑ መስጠት ማለት ነው። አ.ት፡ “ለአሞራውያን ኃይል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አሁን ወዴት መሄድ እንችላለን?

እዚህ ጋ ይህ ጥያቄ ምን ያህል እንደ ፈሩ አጽንዖት ይሰጣል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ምንም መሄጃ የለንም”። (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ልባችን እንዲቀልጥ አደረጉ

ይህ ማለት ፈርተዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “በጣም እንድንፈራ አደረጉን” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እስከ ሰማይ ድረስ የታጠሩ ናቸው

ይህ ከተሞቹ ሰፊና ጠንካራ በመሆናቸው ምክንያት ሰዎቹ ምን ያህል እንደ ፈሩ አጽንዖት የሚሰጥ ግነት ነው። አ.ት፡ “ሰማይ የሚደርሱ የሚመስሉ ግንቦች አሏቸው” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

የኤናቅን ልጆች

እነዚህ የኤናቅ ሕዝብ ተወላጆች ሲሆኑ በጣም ረጃጅምና ኃይለኞች ነበሩ። (See: Assumed Knowl- edge and Implicit Information and ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 1:29

አልኳችሁ

“ለአባቶቻችሁ ነገርኳቸው”

በዐይኖቻችሁ ፊት

እዚህ ጋ ሰዎቹ ስላዩት ነገር አጽንዖት ለመስጠት በ”ዐይኖቻቸው” ተወክለዋል። አ.ት፡ “እናንተ ራሳችሁ ያያችሁት” (See: Synecdoche)

ዐይታችኋል አምላካችሁ እግዚአብሔር ተሸከማችሁ ሄዳችሁ መጣችሁ

ሙሴ፣ እስራኤላውያን አንድ ሰው የሆኑ ይመስል “አንተ” እና “የአንተ” እያለ ይናገራል፤ እነዚህ አገባቦች ሁሉ ነጠላ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

አባት ልጁን እንደሚሸከም አምላካችሁ እግዚአብሔር እናንተን ተሸከማችሁ

እዚህ ጋ እግዚአብሔር ለሕዝቡ የሚያደርግላቸው ክብካቤ ከአባት ጋር ተነጻጽሯል። አ.ት፡ “አባት ልጁን እንደሚንከባከብ አምላካችሁ እግዚአብሔር ተንከባክቧችኃል” (See: Simile)

ወደዚህ ስፍራ እስክተመጡ ድረስ

“እግዚአብሔር ሊሰጣችሁ ቃል ወደገባላችሁ ወደዚህ ምድር እስክትመጡ ድረስ”

Deuteronomy 1:32

በፊታችሁ የሄደ _ አምላካችሁ እግዚአብሔር

ባለፈው ዘመን በጉዞአቸው ሁሉ እግዚአብሔር በእስራኤል ፊት የሄደባቸውን መንገዶች በሙሉ ሙሴ ያስታውሳቸዋል።

ሥፈሩ

“ድንኳኖቻችሁን ትከሉ”

Deuteronomy 1:34

የቃላችሁን ድምፅ ሰማ

“ስትናገሩ የነበረውን ሰማ”

ማለና እንዲህ አለ

በእርሱ ላይ ያመጹት እግዚአብሔር ሊሰጣቸው ቃል ወደ ገባላቸው ምድር እንዳይገቡ ማለ።

ያያሉ

“ይገባሉ”

ካሌብ ብቻ

“ከካሌብ በቀር”

ዮፎኒ

ይህ የካሌብ አባት ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ እግዚአብሔርን ፈጽሞ ተከትሏል

እግዚአብሔር ራሱን እንደ ሌላ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “እርሱ ሙሉ በሙሉ ታዞኛል” (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 1:37

እግዚአብሔር በእናንተ ምክንያት ተቆጣኝ

ይህ የሚያመለክተው ሙሴ በእስራኤል ሕዝብ ላይ በመቆጣቱ ምክንያት እግዚአብሔር እንዲያደርግ የነገረውን ያልታዘዘበትን ጊዜ ነው። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ነዌ

ይህ የኢያሱ አባት ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በፊትህ የሚቆመው

ኢያሱ በሙሴ ፊት ለምን ይቆም እንደነበረ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እንደ አገልጋይህ በፊትህ የሚቆመው” ወይም “የሚረዳህ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 1:39

ክፉና ደጉን የማያውቁት

የትኛው ክፉ እና የትኛው ደግ እንደሆነ ገና የማያውቁ

ተመልሳችሁ ጉዞአችሁን ቀጥሉ

“ወደ ኋላችሁ ተመለሱና በመጣችሁበት መንገድ ተመልሳችሁ ሂዱ”

Deuteronomy 1:41

በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአትን ሠርተዋል

“እርሱን ባለመታዘዝ በእግዚአብሔር ላይ አምጸናል”

እንከተላለን

“እንታዘዛለን”

ኮረብታማውን አገር ለመውጋት

እዚህ ጋ “ኮረብታማው አገር” የተባለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚወክለው በዚያ የሚኖሩትን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “በኮረብታማው አገር የሚኖሩትን ሰዎች ለመውጋት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእናንተ ጋር አልሆንም፣ እናንተም በጠላቶቻችሁ ትሸነፋላችሁ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከእናንተ ጋር ስለማልሆን ጠላቶቻችሁ ያሸንፏችኋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 1:43

ኮረብታማውን አገር ወጉ

“ኮረብታማው አገር” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የቆመው በዚያ ለሚኖሩ ሰዎች ነው። አ.ት፡ “በኮረብታማው አገር የሚኖሩትን ሰዎች ወጉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እንደ ንብ አባረሯችሁ

“ንብ” ትንሽ፣ በራሪ ነፍስ ሲሆን በመንጋ ሆኖ የሚበርና ስጋት የሚሆኑባቸውን ሰዎች የሚነድፍ ነው። ይህ ማለት በጣም ብዙ አሞራውያን የእስራኤል ወታደሮችን ከጦርነቱ እስኪሸሹ ድረስ ወግተዋቸዋል። (See: Simile and የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

ሴይር

ይህ የአንድ አነስተኛ ምድር ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሔርማ

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

መቷችሁ

“ከወታደሮቻችሁ ብዙዎቹን ገደሉ”

Deuteronomy 1:45

ተመለሳችሁና አለቀሳችሁ

“ወደ ቃዴስ ተመለሳችሁና አለቀሳችሁ”


Chapter 2

1 ከዚያም እግዚአብሔርም እንደተናገረኝ ተመልሰን በኤርትራ ባሕር መንገድ ጉዞአችንን በምድረ በዳ ውስጥ ተመለስን፤ 2 በሴይርም ተራራ ዙሪያ ለብዙ ቀናት ተጓዝን። 3 እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ተናገረኝ፦ ይህን ተራራ የዞራችሁበት ይበቃችኋል፤ ተመልሳችሁ ወደ ሰሜን ሄዱ። 4 ሕዝቡንም እንዲህ ብለህ እዘዛቸው፦ በሴይር በሚኖሩ በወንድሞቻችሁ በዔሳው ልጆች ድንበር ታልፋላችሁ፤ እነርሱም ይፈሩአችኋል። 5 ስለዚህ የሴይርን ተራራ ለዔሳው ርስት አድርጌ ስለ ሰጠሁ እኔ ከምድራቸው የጫማ መርገጫ ያህል እንኳ አልሰጣችሁም፥ ከእነርሱም ጋር እንዳትዋጉ እጅግ ተጠንቀቁ።። 6 የምትበሉትንም ምግብ ከእነርሱም በገንዘብ ትገዛላችሁ፤ የምትጠጡትንም ውኃ ደግሞ በገንዘብ ትገዛላችሁ። 7 አምላካችሁ እግዚአብሔር ፤ በዚህ በታላቅ ምድረ በዳ መጓዛችሁን ስላወቀ የእጃችሁን ሥራ ሁሉ ባርኮልሃልና። በእነዚህ አርባ ዓመት ውስጥ አምላካችሁ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ነበረ፥ አንዳችም አልጎደለባችሁም። 8 በሴይርም ከሚኖሩት ከወንድሞቻችሁ ከዔሳው ልጆች በዓረባ መንገድ ከኤላትና ከዔጽዮን ጋብር አለፍን። ተመልሰንም በሞዓብ ምድረ በዳ መንገድ አለፍን። 9 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ ሞዓብን አታስጨንቁአቸው፤ አትውጋቸውም። ምክንያቱም የእነርሱን ምድር ርስት እንዲሆንላችሁ አልሰጣችሁም፤ ዔርን ለሎጥ ልጆች ርስት አድርጌ ሰጠኋችሁ። 10 አስቀድሞ ታላቅና ብዙ ሕዝብ ሆነው እንደ ዔናቅምልጆች በቁመት የረዘሙ ኤሚማውያን በዚያ ይኖሩ ነበር፤ 11 እነርሱም ደግሞ እንደ ዔናቅ ልጆች ራፋይም ይባሉ ነበር፤ ሞዓባውያን ግን ኤሚም ይሉአቸዋል። 12 ሖራውያንም ደግሞ አስቀድሞ በሴይር ላይ ይኖሩ ነበር፥ የዔሳው ልጆች ግን አሳደዱአቸው። እግዚአብሔርም በሰጠው በርስቱ ምድር እስራኤል እንዳደረገ፥ ከፊታቸው አጠፉአቸው፥ በስፍራቸውም መኖር ጀመሩ። 13 እግዚአብሔርም፦ ተነሡ የዘሬድንም ወንዝ ተሻገሩ አለ። የዘሬድንም ወንዝ ተሻገርን። 14 ከቃዴስ በርኔ ከመጠንበት ዘሬድን ወንዝን እስከ ተሻገርንበት ቀኖች ድረስ ሠላሳ ስምንት ዓመታት ነበሩ። እግዚአብሔር እንደ ማለላቸው ለመዋጋት ብቁ የሆኑ ሰዎች ትውልድ ሁሉ ከሕዝብ መካከል የጌድይት በዚያን ጊዜ ነበር። 15 ከዚህ በተጨማሪ፥ ከመሄዳቸው በፊት ከሕዝቡ መካከል ለማጥፋት የእግዚአብሔር እጅ በእነርሱ ላይ ከብዶ ነበረ። 16 ለመዋጋት ብቁ የሆኑት ሁሉ ከሕዝቡ መካከል በሞቱና በጠፉ ጊዜ 17 እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፦ 18 አንተ ዛሬ የሞዓብን ዳርቻ ዔርን ታልፋለህ። 19 ለሎጥም ልጆች ርስት አድርጌ ስለ ሰጠሁ በአሞን ልጆች አቅረቢያ ስትደርስ አታስጨንቁአቸው አትውጋቸውም፤ ምክንያቱም ከአሞን ልጆች ምድር ርስት አልሰጥህምና ። 20 ያም ደግሞ የራፋይም ምድር ተብሎ ተቆጠረ። ራፋይምም አስቀድሞ በዚያ ይኖሩ ነበር፤ 21 አሞናውያን ግን ዛምዙማውያን ብለው የሚጠሩአቸው እንደ ዔናቅም ልጆች ቁመታቸው ረጅም ነበር። 22 እግዚአብሔር ከአሞራውያን ፊት አጠፋቸው፤ እነርሱንም አሳድደው በስፍራቸው ይኖሩ ነበር። ሖራውያንን ከፊታቸው አጥፍተው በሴይር ለሚኖሩት ለዔሳው ልጆች እንዳደረገ እንዲሁ ለእነርሱ አደረገ፤እነርሱም አሳድደው በስፍራቸው እስከ ዛሬ ድረስ ተቀመጡ። 23 እስከ ጋዛ ድረስ ባሉ መንደሮች ይኖሩ የነበሩትን ኤዋውያንን ከከፍቶር የወጡ ከፍቶራውያን አጠፉአቸው፥ በስፍራቸውም ኖሩ። 24 ደግሞም አለ፦ ተነሥታችሁ ሂዱ፥ የአርኖንንም ሸለቆ ተሻገሩ፤ እነሆ አሞራዊውን የሐሴቦንን ንጉሥ ሴዎንንና ምድሪቱን በእጅህ አሳልፌ ሰጥቻለሁ። እርስዋን ለመውረስ ጀምር፥ ከእርሱም ጋር ተዋጋ። 25 ከሰማይ በታች ባሉ አሕዛብ ሁሉ ላይ ማስደንገጥህንና ማስፈራትህን እሰድድ ዘንድ ዛሬ እጀምራለሁ፤ ወሬህን በሰሙ ጊዜ በፊትህ ይንቀጠቀጣሉ፥ ድንጋጤም ይይዛቸዋል። 26 ከቅዴሞትም ምድረ በዳ የሰላምን ቃል ይነግሩት ዘንድ ወደ ሐሴቦን ንጉሥ ወደ ሴዎን እንዲህ ብዬ መልእክተኞችን ላክሁ፦ 27 ወደ ቀኝና ግራ ሳልል በአገርህ ላይ በአውራ ጎዳና ልለፍ። 28 የምበላውን ምግብ በገንዘብ ሽጥልኝ፥ የምጠጣውንም ውኃ በገንዘብ እንድገዛ ስጠኝ፤ 29 በሴይር የሚኖሩ የዔሳው ልጆች፥ በዔርም የሚኖሩ ሞዓባውያን እንዳደረጉልኝ አምላካችን እግዚአብሔር ወደሚሰጠን ምድር ዮርዳኖስን እስክሻገር ድረስ ብቻ በእግሬ ልለፍ። 30 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ዛሬው ሁሉ በእጃችሁ አሳልፎ ይሰጣችሁ ዘንድ ልቡን ስላደነደነና ስላጸና የሐሴቦን ንጉሥ ሴዎን ግን ያሳልፈን ዘንድ አልፈቀደም ። 31 እግዚአብሔርም፦ እነሆ ሴዎንንና ምድሩን በእጅህ አሳልፌ መስጠት ጀመርሁ ምድሩን ትገዛት ዘንድ መውረስ ጀምር አለኝ። 32 ሴዎንም ሕዝቡም ሁሉ ሊጋጠሙን ወደ ያሀጽ ወጡ። 33 እግዚአብሔር አምላካችንም አሳልፎ ስለሰጠን አሸነፈነው፥እርሱንና ልጆቹን፥ ሕዝቡንም ሁሉ እስኪሞቱ ድረስ አሸነፍን፤መታንም። 34 በዚያን ጊዜም ከተሞቹን ሁሉ ወሰድን የተቀመጡባቸውንም ሰዎች ሁሉ ሴቶችንና ሕፃናትን አንዳችም ሳናስቀር አጠፋን። 35 ከብቶቻቸውንና በከተሞቻቸው ያሉትን ብቻ ብዝበዛ ለራሳችን ወሰድን። 36 በአርኖን ቆላ ጫፍ ካለው ከአሮዔር ከሸለቆውም ውስጥ ካለው ከተማ ጀምረን እስከ ገለዓድ ድረስ ማናቸውም ከተማ ከእኛ በላይ አልሆነም። እግዚአብሔር አምላካችን በፊታችን ባሉት ጠላቶቻችን ላይ ድልን ሰጠን። 37 ዳሩ ግን አምላካችን እግዚአብሔር ወደ ከለከለን ወደ አሞን ልጆች ምድር በያቦቅም ወንዝ አጠገብ ወዳለው ስፍራ ሁሉ በተራራማው አገር ወዳሉት ከተሞች አልደረስንም።



Deuteronomy 2:1

ከዚያም ተመለስንና ጉዞአችንን ቀጠልን

“ከዚያም ተመለስንና ሄድን”

ለብዙ ቀናት በሴይር ተራራ አጠገብ ሄድን

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) እስራኤላውያን ሴይር ተብሎ በሚጠራው ተራራ አቅራቢያ ለረጅም ጊዜ ተጉዘዋል ወይም 2) እስራኤላውያን ሴይር ተብሎ በሚጠራው ተራራ አካባቢ ለረጅም ጊዜ ተቅበዝብዘዋል።

የሴይር ተራራ

ይህ ከሙት ባህር በስተደቡብ የሚገኝ ተራራማ አካባቢ ነው። አካባቢው “ኤዶም” በመባልም ይጠራል። ይህንን በዘዳግም 1፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ብዙ ቀናት

ይህንን አንዳንድ ቋንቋዎች “ብዙ ሌሊቶች” ብለው ይተረጉሙታል።

Deuteronomy 2:4

ወንድሞቻችሁ የኤሳው ተወላጆች

“ዘመዶቻችሁ የኤሳው ተወላጆች”

የሴይርን ተራራ ርስት አድርጌ ለኤሳው ሰጥቸዋለሁ

እግዚአብሔር ለኤሳው ተወላጆች ይህንን ክልል እንደ ሰጣቸው እስራኤላውያንን ያስታውሳቸዋል።

Deuteronomy 2:6

ከእነርሱ ምግብ ትገዛላችሁ

እግዚአብሔር የሚሰጣቸው ትዕዛዝ ሳይሆን ፈቃድ ወይም መመሪያ ነው፣ እንዳይሰርቁም ይነግራቸዋል። “ከእነርሱ ምግብ እንድትገዙ እፈቅድላችኋለሁ” ወይም “ምግብ ከፈለጋችሁ ከእነርሱ መግዛት ይኖርባችኋል”

ከእነርሱ

“ከኤሳው ተወላጆች”

በገንዘብ

ይህ ቃል የማያስፈልግ ወይም ትርጉሙን ግልጽ የማያደርግ ከሆነ መተው ይኖርብህ ይሆናል።

አምላክህ ባርኮሃል _ እጅህ _ አካሄድህ _ አምላክህ _ ከአንተ ጋር እና አላጣህም

ሙሴ እስራኤላውያንን አንድ ሰው እንደሆኑ ዓይነት አድርጎ ይናገራል፣ በመሆኑም “አንተ” እና “የአንተ” ተብለው የተነገሩት ሁሉ ነጠላ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

በእጅህ ሥራ ሁሉ

የ “እጅህ ሥራ” የሚያመለክተው ያደረጉትን ሥራ ሁሉ ነው። አ.ት፡ “ሥራህን ሁሉ” (See: Synec- doche)

በመንገዳችሁ ጠብቋችኋል

እዚህ ጋ ሕዝቡ ሲጓዙ የደረሰባቸው እንደ “መንገድ” ተነግሯል። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አርባ ዓመታት

“40 ዓመታት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ምንም አላጣችሁም

ይህ “የምትፈልጉት ሁሉ ነበራችሁ” የተጋነነ አባባል ነው። (የተጋነነ አባባል የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 2:8

በወንድሞቻችን

“በዘመዶቻችን”

ኤላት _ ጽዮን ጋብር

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ተመለስን

ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “መጓዛችንን ቀጠልን” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 2:9

ሞዓብን አታስቸግሩት

“ሞዓብ” የሚለው ቃል የሚወክለው የሞዓብን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “የሞዓብን ሕዝብ አታስቸግሯቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዔር

ይህ በሞዓብ የሚገኝ የአንድ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የሎጥ ተወላጆች

የእስራኤል ሕዝብ ከሞዓብ ተወላጆች ጋር ዝምድና ነበራቸው። ሞዓብ የሎጥ ልጅ ነበር። ሎጥ ደግሞ የአብርሃም የወንድም ልጅ ነበር። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 2:10

ኤሚማውያን ይኖሩባት ነበር _ ኤሚም ብለው ይጠሯቸዋል

እነዚህ ቃላት ከሞዓባውያን በፊት በምድሪቱ ላይ ስለነበሩት ስለ ኤሚም ሕዝብ ዳራዊ መረጃ ይሰጣሉ። ቋንቋህ ዳራዊ መረጃን ለማመልከት የተለየ መንገድ ይኖረው ይሆናል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ኤሚማውያን _ ራፋይም

እነዚህ ግዙፍ እንደሆኑ የሚታሰቡ የሕዝብ ወገን ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዔናቅ

እነዚህ በጣም ረጃጅምና ኃይለኞች የነበሩ የዔናቅ ሕዝቦች ተወላጆች ናቸው። ይህንን በዘዳግም 1፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 2:12

ሖራውያን

ይህ የአንድ የሕዝብ ወገን ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከፊታቸው አጠፏቸው

“ከእነርሱ ጋር አንዱም በሕይወት እንዳይኖር ሁሉንም ገደሏቸው” ወይም “ሁሉንም በመግደል ከአጠገባቸው አስወገዷቸው”

Deuteronomy 2:13

ስለዚህ ‘አሁን ተነሡ _ ዜሬድ’

“ከዚያም እግዚአብሔር፣ “አሁን ተነሡ _ ዜሬድ’ ስለዚህ”። ይህ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ከዚያም እግዚአብሔር ተነሥተን _ ዜሬድ ተናገረን። ስለዚህ” (ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

ተነሡ

አንድ ነገር ለማድረግ ጀምሩ (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የዜሬድን ጅረት

ይህ ምንጭ ከደቡብ ምስራቅ ወደ ሙት ባህር በመፍሰስ በኤዶምና በሞዓብ መካከል ድንበር ያበጃል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አሁን ቀኖቹ

“አሁን” የሚለው ቃል ከትረካው የእስራኤል ሕዝብ ለምን ያህል ጊዜ እንደተጓዙና በዚያ ትውልድ ላይ እግዚአብሔር ወደተቆጣበት ዳራዊ መረጃ መቀየሩን ያመለክታል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ሠላሳ ስምንት ዓመት

“38 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ከሕዝቡ ተለይተው ሄደው ነበር

ይህ “ሞተው ነበር” የሚል የትህትና አነጋገር ነው። (See: Euphemism)

የእግዚአብሔር እጅ በእነርሱ ላይ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር እጅ” የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ኃይል ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ኃይሉን በእነርሱ ላይ ተጠቅሟል” ወይም “እግዚአብሔር ቀጣቸው” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 2:16

እናንተ ናችሁ - መጣችሁ - አታስቸግሯቸው - አልሰጣችሁም

ሙሴ ለእስራኤላውያን አንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ በመሆኑም “አንተ” እና “አታስቸግሯቸው” የሚልበት ትዕዛዝ አገባብ ሁሉ ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

ዔርን ታልፋላችሁ

ይህ በሞዓብ የሚገኝ የአንድ ከተማ ስም ነው። “ዔር”ን በዘዳግም 2፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ለሎጥ ተወላጆች

የእስራኤል ሕዝብ ከአሞን ተወላጆች ጋር ዝምድና ነበራቸው። አሞን የሎጥ ልጅ ነበር። ሎጥ ደግሞ የአብርሃም የወንድሙ ልጅ ነበር። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 2:20

ያ ደግሞ ይቆጠር ነበር

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ሰዎች ያንን ደግሞ ይቆጥሩ ነበር”። (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ረፋይም

ይህ የአንድ ሕዝብ ወገን ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዘምዙማውያን

ይህ የረፋይም ሕዝብ ወገን ሌላው ስማቸው ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዔናቅ

ይህ የአንድ ሕዝብ ወገን ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በአሞናውያን ፊት አጠፋቸው

“አሞናውያን እንዲያሸንፏቸው ፈቀደላቸው” ወይም “አሞናውያን ሁሉንም እንዲገድሏቸው ፈቀደላቸው”

እነርሱ ተኳቸው፣ በእነርሱ ስፍራም ኖሩ

“አሞናውያኑ ረፋይማውያን የነበራቸውን ሁሉ ወሰዱባቸው፣ ረፋይማውያን ይኖሩ በነበሩበትም ስፍራ ኖሩ”

ሖራውያን

ይህ የአንድ ሕዝብ ወገን ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡12 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ተኳቸው፣ በእነርሱ ስፍራም ኖሩ

“ሖራውያን የነበራቸውን ሁሉ ወሰዱባቸው፣ ሖራውያን ይኖሩ በነበሩበትም ስፍራ ኖሩ”

Deuteronomy 2:23

ኤዋውያን - ከፍቶር

እነዚህ የሕዝብ ወገን ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከፍቶር

x

Deuteronomy 2:24

አሁን ተነሡ

ሕዝቡ ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔር ለሙሴ እየነገረው ነው። “አሁን ተነሡ” ወይም “አሁን ሂዱ”

መንገዳችሁን ሂዱ

“ጉዞአችሁን ቀጥሉ”

የአርኖን ሸለቆ

ይህ የአርኖን ወንዝ ሸለቆ ስም ነው። እርሱ በሞዓብና በአሞራውያን መካከል ድንበር ያበጃል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በእጃችሁ ሰጥቻችኋለሁ

“በእጃችሁ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ትርጉም “በቁጥጥራችሁ ወይም በኃይላችሁ ሥር” ማለት ነው። አ.ት፡ “እንድታሸንፉ ኃይልን ሰጥቻችኋለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እጃችሁ - ለመውረስ ጀምሩ - ተዋጉ - ማስፈራታችሁ - ዝናችሁ - በእናንተ ምክንያት

ሙሴ ለእስራኤላውያን አንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ በመሆኑም “አንተ” እና “የእናንተ” እንዲሁም ትዕዛዝ የሆኑት “ለመውረስ ጀምሩ” እና “ተዋጉ” ሁሉም አገባቦች ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

ሴዎን

ይህ የአንድ ንጉሥ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሐሴቦን

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከእርሱ ጋር ተዋጋ

“ከእርሱና ከሰራዊቱ ጋር ተዋጋ”

አስፈሩ፣ አስደንግጡም

“ፍርሐት” እና “ድንጋጤ” የሚሉት ቃላት መሠረታዊ ትርጉማቸው አንድ ቢሆንም ፍርሐቱ ታላቅ መሆኑን አጽንዖት ይሰጣል። አ.ት፡ “ከባድ ፍርሐት ጣሉባቸው” (See: Doublet)

ከሰማይ በታች ያለ ሕዝብ ሁሉ

ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “በየአገሩ ያሉ ሕዝቦች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ይንቀጥቀጡና ይጨነቁ

ይህ ሕዝቡ በጭንቀት እንደሚንቀጠቀጡ አጽንዖት ይሰጣል። (See: Hendiadys)

Deuteronomy 2:26

እኔ ላክኋቸው

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው ሙሴን ነው።

ወደ ቄድሞት ምድረ በዳ

ይህ በአርኖን ሸለቆ አቅራቢያ የሚገኝ ቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሴዎን -- ሐሴቦን

ይህ የሰውና የቦታ ስም ነው። እነዚህን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በሰላም ቃል

“ሰላምን ባቀርብላቸው” ወይም “ስለ ሰላም ከሚጠይቅ መልዕክቴ ጋር”

ወደ ቀኝም ሆነ ወደ ግራ ዘወር አልልም

ይህ ሐረግ ሁሌም በአንድ አቅጣጫ እንደሚሄዱ አጽንዖት ይሰጣል። ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። “አቅጣጫዬን አልቀይርም” ወይም “ሁሌም መስመሬን ጠብቄ እጓዛላሁ” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 2:28

የምበላውን ምግብ በገንዘብ ትሸጥልኛለህ፤ የምጠጣውንም ውሃ በገንዘብ ስጠኝ

ሙሴ እስራኤላውያን ከአሞራውያን እንደማይሰርቁና ሴዎንና ሕዝቡ ምግብና ውሃ እንዲሸጡላቸው ሴዎንን ይጠይቀዋል እንጂ ትዕዛዝ አይሰጠውም። አ.ት፡ “ለምበላው ምግብና ለምጠጣው ውሃ መክፈል እንዳለብኝ አስባለሁ”

እንድበላ - ሽጥልኝ - እንድጠጣ - ስጠኝ

ሙሴ ስለራሱ አድርጎ የሚናገረው እስራኤላውያንን ሲያመለክት ነው። አ.ት፡ “እንበላው ዘንድ - ለእኔና ለሕዝቤ ሽጥልኝ - እንጠጣው ዘንድ - ስጠን” (See: Synecdoche)

በእግሬ እንዳልፍ ብቻ ፍቀድልኝ

“በምድርህ ተራምደን ብቻ እንለፍ”

ዔር

ይህ የቦታ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 2:30

ሴዎን - ሐሴቦን

ይህ የሰውና የቦታ ስም ነው። እነዚህን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አምላካችሁ -- ጉልበታችሁ

ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራል፣ ስለዚህ በሁሉም አገባብ “ያንተ” የሚለው ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

አሳቡን አደነደን፣ ልቡንም ግትር አደረገ

ሁለቱም ሐረጎች ትርጉማቸው ተመሳሳይ ሲሆን አጽንዖት የሚሰጠው እግዚአብሔር “በጣም ግትር እንዲሆን አደረገው” ለማለት ነው። (See: Parallelism)

ሴዎንን እና ምድሩን በፊትህ አሳልፌ ልሰጥ

“ሴዎንን እና ምድሩን ለአንተ ልሰጥህ”

ምድሩ ለአንተ ይሆን ዘንድ ለመውረስ ጀምር

“ትወርሰው ዘንድ የእርሱን ምድር ለራስህ ውሰድ”

Deuteronomy 2:32

ሴዎን

ይህ የአንድ ንጉሥ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ያሀጽ

ይህ ሞዓብ ውስጥ የነበረ የአንድ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 2:34

የእርሱን ከተሞች ሁሉ ወሰድን

“የንጉሥ ሴዎንን ከተሞች በሙሉ ያዝን”

እያንዳንዱን ከተማ ፈጽሞ አጠፋን

“በየከተማው ይኖሩ የነበሩትን ሰዎች ሁሉ ገደልን”

Deuteronomy 2:36

አሮዔር

ይህ በአርኖን ወንዝ ሰሜናዊ ዳርቻ የሚገኝ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የአርኖን ሸለቆ

“አርኖን” የወንዝ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡24 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ለእኛ ከባድ የሆነ ከተማ አልነበረም

ይህ አሉታዊ አገላለጽ በጦርነት የነበራቸው ስኬት ላይ አጽንዖት ለመስጠት ጥቅም ላይ ውሏል። ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ምንም እንኳን ከተማው ዙሪያው በረጃጅም ቅጥር የታጠረ ቢሆንም በየከተማው ያሉትን ሕዝቦች ማሸነፍ ችለናል። (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

አልሄዳችሁም

ሙሴ እስራኤላውያኑን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ” ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

የያቦቅ ወንዝ

ይህ በሴዎን እና በአሞናውያን ምድር መካከል ድንበር ያበጀ ወንዝ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 3

1 ተመልሰን በባሳን መንገድ ሄድን፥ የባሳን ንጉሥ ዐግና ሕዝቡ ሁሉ በኤድራይ ሊዋጉን መጡ። 2 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ እርሱንና ሕዝቡን ሁሉ ምድሩንም በእጅህ አሳልፌ ሰጥቼአለሁና አትፍራው። በሐሴቦን ይኖር በነበረው በአሞራውያን ንጉሥ በሴሶን ላይ እንዳደረግህ በእርሱም ታደርግበታለህ አለኝ። 3 እግዚአብሔር አምላካችንም በባሳን ንጉሥ በዐግ ሕዝቡንም ሁሉ በእጃችን ድልን ሰጠን። እኛም አንድ እንዳይቀር እስኪሞቱ ድረስ መታነው። 4 በዚያን ጊዜም አንድም ያልወሰድነው ሳይቀር ሁሉንም ስድሳ ከተሞችን፦ በባሳን ያለውን የዐግን መንግሥት፥ የአርጎብን አገር ሁሉ ከተሞችን ወሰድን። 5 እነዚህም ከተሞች ሁሉ ዙሪያቸው በረጅም ቅጥር፥ በበሮቻቸውና በመወርወሪያዎች የተመሸጉ ነበር፤ በአጠገባቸውም ብዙ ያልተመሸጉት ከተሞች ነበሩ። 6 በሐሴቦንም ንጉሥ በሴዎን እንዳደረግን ከወንዶችና ሴቶች ከሕፃናትም ጋር ፈጽሞ አጠፋናቸው። 7 ነገር ግን ከአጠፋናቸው ከተሞች ሁሉ ከብቶቹን ሁሉ ምርኮም ለራሳችን ወሰድን። 8 በዚያም ጊዜ ከአርኖን ሸለቆ ጀምሮ እስከ አርሞንዔም ተራራ ድረስ ምድሪቱን ከዮርዳኖስ ማዶ ከነበሩ ከሁለቱ ከአሞራውያን ነገሥታት እጅ ወሰድን፤ 9 (ሲዶናውያን አርሞንዔምን ሢርዮን ብለው ይጠሩታል፥ አሞራውያንም ሳኔር ብለው ይጠሩታል) ፤ 10 በሜዳውም ያሉትን ከተሞች ሁሉ፥ ገለዓድንም ሁሉ፥ በባሳንም ያሉትን የዐግን መንግሥት ከተሞች እስከ ስልካና፤እስከ ኤድራይ ድረስ ባሳንን ሁሉ ወሰድን። 11 ከራፋይም ወገን የባሳን ንጉሥ ዐግ ብቻውን ተርፎ ነበር፤ እነሆም አልጋው የብረት አልጋ ነበረ፤ እርሱ በአሞን ልጆች አገር በረባት አልኖረምን? ይህም በሰው ክንድ ልክ ርዝመቱ ዘጠኝ ክንድ፥ ወርዱም አራት ክንድ ነበረ። 12 በዚያን ጊዜ በአርሞን ሸለቆ ከአሮዔር ርስት አድርገን የወሰደነውን ይህን የገለዓድን ተራራማ ምድር እኩልታ ከተሞቹንም ለሮቤልና ለጋድ ነገድ ሰጠኋቸው። 13 ከገለዓድም የቀረውን የዐግንም መንግሥት ባሳንን ሁሉ የአጎብንም ምድር ሁሉ ለምናሴ ነገድ እኩሌታ ሰጠሁ። (ይህም ተመሳሳይ አገር የራፋይም ምድር ተብሎ ይቆጠራል።) 14 የምናሴ ነገድ አንዱ ኢያዕር እስከ ሄሸራውያንና እስከ ማዕካታውያን ዳርቻ ድረስ የአርጎብን አካባቢ ሁሉ ወሰደ። ይህንም የባሳንን ምድር እስከ ዛሬ ድረስ የሚጠራውን በስሙ የኢያዕር መንደሮች ብሎ ጠራ። 15 ለማኪርም ገለዓድን ሰጠሁት። 16 ለሮቤል ነገድና ለጋድም ነገድ ከገለዓድ ጀምሮ እስከ አርግኖን ሸለቆ ድረስ የሸለቆውን እኩሌታ ዳርቻውንም እስከ አሞን ልጆች ዳርቻ እስከ ያቦቅ ወንዝ ድረስ ሰጠኋቸው። 17 ከኪኔሬት እስከ ዓርባ ባሕር (እርሱም የጨው ባሕር) ድረስ ከፈስጋ ተራራ በታች ወደ ምሥራቅ ያለውን የዮርዳኖስን ሸለቆ ዳቻውንም ሰጠኋቸው። 18 በዚያም ጊዜ እንዲህ ብዬ አዘዝኋችሁ፦ እግዚአብሔር አምላካችሁ ይህን ምድር ርስት አድርጎ ሰጥቶአችኋል፤ እናንተ የጦር ሰዎች መሣሪያችሁን ታጥቃችሁ በወንድሞቻችሁ ከእስራኤል ልጆች ፊት ታልፋላችሁ። 19 ነገር ግን ሚስቶቻችሁ፥ ልጆቻችሁና ከብቶቻችሁ (ብዙ ከብቶች እንዳሉአችሁ አውቃለሁ) በሰጠኋችሁ ከተሞች ይቀመጣሉ፤ 20 ይኸውም እግዚአብሔር እናንተን እንዳሳረፈም ወንድሞቻችሁን እስኪያሳርፍ ድረስ እነርሱም ደግሞ በዮርዳኖስ ማዶ እግዚአብሔር አምላካችሁ የሚሰጣቸውን ምድር እስኪወርሱ ድረስ ነው፤ ከዚያም በኋላ እናንተ ሁላችሁ ወደ ሰጠኋችሁ ርስት ትመለሳላችሁ። 21 በዚያም ጊዜ ኢያሱን እንዲህ ብዬ አዘዝሁት፦አምላካችሁ እግዚአብሔር በእነዚህ በሁለቱ ነገሥታት ያደረገውን ሁሉ ዓይኖችህ አይተዋል፤ እንዲሁ በምታልፍባቸው መንግሥታትም ሁሉ ላይ እግዚአብሔር ያደርጋል። 22 አምላካችሁ እግዚአብሔር እርሱ ስለ እናንት ስለሚዋጋ አትፈራቸውም ብዬ አዘዝሁት። 23 በዚያም ጊዜ እኔ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብዬ ለመንሁ፦ 24 ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፥ ታላቅነትህንና ብርቱ እጅህን ለእኔ ለባሪያህ ማሳየት ጀምረሃል፤ በሰማይ ወይም በምድር እንደ አንተ፥ እንደ ኃይልህ፥ ያደርግ ዘንድ የሚችል አምላክ ማን ነው? 25 እኔም ወደዚያ ልሂድና በዮርዳኖስም ማዶ ያለውን መልካሙን ምድርና መልካሙን ተራራማውን አገር ሊባኖስንም ለመየት እለምንሃለሁ። 26 እግዚአብሔር ግን እናንተ ባለመስማታችሁ ምክንያት ተቆጣኝ። እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ ስለዚህም ነገር ደግመህ እንዳትናገረኝ ይበቃሃል። 27 ይህን ዮርዳኖስን ስለማትሻገር ወደ ፈስጋ ራስ ውጣና ዓይንህንም ወደ ምዕራብ፥ ወደ ሰሜን፥ ወደ ደቡብምና ወደ ምሥራቅ ዓይንህን አንሥተህ ተመልከት። 28 በዚህ ፈንታ ኢያሱን አስተምራው፥ አደፋፍረው እንዲሁም አጽናው፤ ምክንያቱም እርሱ በዚህ ሕዝብ ፊት ይሄዳል፥ አንተም የምታየውን ምድር ያወርሳቸዋል። 29 ስለዚህም በቤተ ፌጎርም በሸለቆው ውስጥ ቆየን።



Deuteronomy 3:1

ዐግ - ሴዎን

እነዚህ የነገሥታት ስሞች ናቸው። እነዚህን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ኤድራይ -- ሐሴቦን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። እነዚህ በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፣ “አትፍራው -- ሰጥቼሃለሁ -- በቁጥጥርህ ስር -- በሐሴቦን -- እንዳደረግኸው

እግዚአብሔር ሙሴ እስራኤላውያንን እንደሆነ ያህል ይናገረዋል፣ ስለዚህ “አትፍራ” የሚለው ትዕዛዝና “አንተ” እና “የአንተ” የሚለው አገባብ ሁሉ ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

አትፍራው -- በእርሱ ላይ -- ሕዝቡንና ምድሩን

እዚህ ጋ “እርሱን” እና “የእርሱ” የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት ዐግን ነው።

ድልን ሰጥቼሃለሁ

እግዚአብሔር ሊያደርግ ያለውን አስቀድሞ እንዳደረገው ቆጥሮ ይናገራል። (See: Predictive Past)

በሴዎን ላይ እንዳደረግኸው በእርሱ ላይ ታደርጋለህ

“በእርሱ” የሚለው ቃል”በእርሱ ሕዝብ ላይ” ለሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ሴዎንን እንዳደረግኸው ዐግንና ሕዝቡን ታጠፋቸዋለህ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 3:3

ሕዝቡ ሁሉ በቁጥጥራችን ሥር ሆነ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የዐግን ሕዝብ በሙሉ በቁጥጥራችን ሥር አደረገ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የእርሱ ከሆነው ሕዝብ አንድም አልቀረለትም

አስራኤላውያን ማንንም በሕይወት እንዳላስቀሩ አጽንዖት ለመስጠት ይህ ምጸት ጥቅም ላይ ውሏል። አ.ት፡ “የእርሱ የሆነው ሕዝብ ሁሉ ሞተ” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

ከስልሳዎቹ ከተሞች ያልወሰድነው አንድም አልነበረም

ይህ 60ዎቹን ከተሞች በሙሉ ስለመውሰዳቸው አጽንዖት የተሰጠበት ድርብ አሉታ ነው። አ.ት፡ “እያንዳንዱን ስልሳ ከተማ ወሰድን” (ድርብ አሉታ የሚለውን ተመልከት)

ስልሳ ከተሞች

“60 ከተሞች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የአርጎብን አካባቢ

ይህ በባሳን ውስጥ ያለ የአንድ አካባቢ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 3:5

እነዚህ ከተሞች በሙሉ በግምብ የታጠሩ ነበሩ

“እነዚህ ከተሞች በሙሉ በ -- የተጠበቁ ነበሩ”

በጣም ብዙ ከሆኑት ጋር

“በጣም ብዙ ከሆኑት በተጨማሪ” ወይም “በጣም ብዙ የሆኑትን ሳይጨምር”

ሴዎን

ይህ የአንድ ንጉሥ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሐሴቦን

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እያንዳንዱን ከተማ በማጥፋት

“በየከተማው የሚኖሩትን ሰዎች በሙሉ በመግደል”

Deuteronomy 3:8

ከሁለቱ ነገሥታት እጅ

እዚህ ጋ “ከእጃቸው” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር “ከቁጥጥራቸው” ማለት ነው። አ.ት፡ “ከሁለት ነገሥታት ቁጥጥር” ወይም “ከሁለቱ ነገሥታት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አሞራውያን -- ባሳን -- ኤድራይ -- ዐግ

“የአሞራዊ ሕዝቦች -- የባሳን ምድር -- የኤድራይ ከተማ -- ንጉሥ ዐግ”። እነዚህን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

በዮርዳኖስ ማዶ

ይህ ከእስራኤል በስተምስራቅ ከዮርዳኖስ ወንዝ ባሻገር ያለውን ምድር ያመለክታል። ሙሴ ይህንን በሚናገርበት ጊዜ ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ ነበር። ይህንን በዘዳግም 1፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ”

በአርኖን ሸለቆ

እነዚህን ቃላት በዘዳግም 2፡24 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

የአርሞንዔም ተራራ -- ሢርዮን -- ሳኔር

እነዚህ በሙሉ ከባሳን በስተሰሜን ዳርቻ ላይ ያለው የአንድ ተራራ ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በሜዳ

ይህ በአርኖን ወንዝና በገለዓድ ተራራ መካከል ያለ ረጅምና ሰፊ ስፍራ ነው።

ሰልካ

ይህ በኤድሪ አቅራቢያ የምትገኝ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 3:11

የትሩፉ -- ሰዎች በሚለኩበት

ይህ የንጉሥ ዐግ ዳራዊ መረጃ ነው። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ራፋይም

ይህንን በዘዳግም 2፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ተመልከት!

“ለምነግርህ ጠቃሚ ነገር ትኩረት ስጥ”።

የሚኖረው -- በረባት አልነበረም?

ጸሐፊው የእስራኤል ሕዝብ ወደ ረባት እንዲሄዱና ዐግ ምን ያህል ታላቅ እንደነበረ ያዩ ዘንድ ለማስታወስ ጥያቄ ያቀርባል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) “የሚኖረው -- በረባት ነበር” ወይም “በረባት -- ይኖራል” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ክንድ

አንድ ክንድ 46 ሴንቲ ሜትር ይረዝማል። (መጽሐፍ ቅዱሳዊ የርቀት መለኪያ የሚለውን ተመልከት)

ሰዎች በሚለኩበት መንገድ

“አብዛኛው ሰው በሚጠቀምበት የክንድ መለኪያ”

Deuteronomy 3:12

አሮዔር

የዚህን ከተማ ስም በዘዳግም 2፡36 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የአርኖን ሸለቆ

እነዚህን ቃላት በዘዳግም 2፡24 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

የአርጎብን ክልል

እነዚህን ቃላት በዘዳግም 3፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ያው ወሰን የራፋይም ምድር ተብሎ ይጠራል

ጸሐፊው የእስራኤል ሕዝብ ስለ ያዙት ምድር ዳራዊ መረጃ ማቅረብ ይጀምራል። የአንተ ቋንቋ ቀጥሎ የሚመጣው ዳራዊ መረጃ መሆኑን የሚያሳይበት መንገድ ካለ እርሱን እዚህ ጋ መጠቀም አለብህ። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ራፋይም

የዚህን ምድር ስም በዘዳግም 2፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 3:14

ኢያዕር

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ጌሹራውያን እና ማዕካታውያን

እነዚህ ከባሳን በስተምዕራብ የሚኖሩ የሕዝብ ወገን ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሓቦት ኢያዕር

ተርጓሚዎች የሚከተለውን የግርጌ ማስታወሻ ያደርጉ ይሆናል፡ “ ‘ሓቦት ኢያዕር’ ማለት ‘የኢያዕር የድንኳን መንደሮች’ ወይም ‘የኢያዕር ግዛት’ ማለት ነው”።

Deuteronomy 3:15

ሰጠሁ

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው ሙሴን ነው።

ለማኪር

ማኪር የምናሴ ልጅ ነበር። እርሱ ሙሴ ይህንን ምድር ከመስጠቱ በፊት ሞቶ ነበር። ስሙ ለሰውየው ተወላጆች ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ለማኪር ተወላጆች” (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የአርኖን ሸለቆ

ይህ የአርኖን የወንዝ ሸለቆ ስም ነው። እርሱ በሞዓብና በአሞራውያን መካከል ድንበር ያበጃል። ይህንን በዘዳግም 2፡24 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የያቦቅ ወንዝ

ይህ በሴዎን ምድር እና በአሞናውያን ምድር መካከል ድንበር ያበጀ ወንዝ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡37 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 3:17

ሌላው ወሰኑ ደግሞ

“የሮቤላውያን እና የጋዳውያን ድንበር ምዕራባዊ ወሰናቸው ነው”

ኪኔሬት

የኪኔሬት ባህር “የገሊላ ባህር” ወይም “የጌንሳሬጥ ሐይቅ” ተብሎም ይጠራል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የፈስጋ ተራራ

ይህ ከአባሪም ሰንሰለታማ ተራራ በስተሰሜን የሚገን የተራራ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 3:18

በዚያን ጊዜ አዘዝኋችሁ

ሌሎች እስራኤላውያን እግዚአብሔር ተስፋ የሰጣቸውን የቀረውን ምድር ድል ያደርጉ ዘንድ የሮቤል ነገድ፣ የጋድ ነገድና ከፊሉ የምናሴ ነገድ እንዲያግዟቸው ሙሴ ያስታውሳቸዋል (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

መሣሪያችሁን ይዛችሁ በፊታቸው ታልፋላችሁ

“የጦር መሣሪያዎቻችሁን ትይዙና ቀድማችሁ የዮርዳኖስን ወንዝ ትሻገራላችሁ”

ወንድሞቻችሁ የእስራኤል ሰዎች

“እስራኤላውያን ባልንጀሮቻችሁ”

Deuteronomy 3:19

እግዚአብሔር ለወንድሞቻችሁ እረፍትን እስኪሰጥ

ጸሐፊው የማረፍን ችሎታ በስጦታ እንደሚሰጥ ቁሳዊ አካል አድርጎ ይናገራል። በተጨማሪም፣ “ማረፍ” የሚለው ቃል ጦርነት የሌለበትን ሰላማዊ ኑሮ የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ወድሞቻችሁ እንዲያርፉ እግዚአብሔር ይፈቅዳል” ወይም “በጦርነት መዋጋትን አቁመው በሰላም እንዲኖሩ እግዚአብሔር ለወንድሞቻችሁ ይፈቅዳል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከዮርዳኖስ ማዶ

ይህ ከእስራኤል በስተምስራቅ ከዮርዳኖስ ወንዝ ባሻገር ያለውን ምድር ያመለክታል። ሙሴ ይህንን በሚናገርበት ጊዜ ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ ነበር። በዘዳግም 1፡1 ላይ እነዚህን ቃላት እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ”

ከዚያም ትመለሳላችሁ

እግዚአብሔር ለእነዚህ ሦስት ነገዶች ምድራቸውን እንዲወርሱ ከመፍቀዱ በፊት ሌሎቹ ነገዶች መሬታቸውን መውረስ እንዳለባቸው ሙሴ አጽንዖት ይሰጣል። “የምትመለሱት ከዚያ በኋላ ብቻ ነው”።

Deuteronomy 3:21

ዕይኖችህ ዓይተዋል

እዚህ ጋ “ዐይኖችህ” የሚያመለክተው ኢያሱን ነው። አ.ት፡ “አንተ ዐይተሃል” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 3:23

ለመንሁ

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው ሙሴን ነው። ይህ ማለት በጣም ቅንና ስሜታዊ በሆነ መንገድ እግዚአብሔርን ጠይቆታል።

ለአገልጋይህ ለማሳየት

እዚህ ጋ “አገልጋይህ” የሚለው ቃል ለአንድ ታላቅ ሥልጣን ላለው በትህትና የመናገር መንገድ ነው። አ.ት፡ “ለአገልጋይህ ልታሳየኝ”

ብርቱ እጅህ

እዚህ ጋ ፈሊጣዊ የሆነው “እጅ” መቆጣጠር ወይም ኃይል ማለት ነው። አ.ት፡ “ኃይልህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ማድረግ የሚችል አምላክ ማነው?

ሙሴ እግዚአብሔር ያደረጋቸውን ሥራዎች ለማድረግ ኃይል ያለው ብቸኛው አምላክ እርሱ መሆኑን አጽንዖት ለመስጠት በጥያቄ መልክ ያቀርባል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “. . . የሚያደርግ ሌላ አምላክ የለም”። (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

በሰማይ ወይም በምድር ላይ

የእነዚህ ሁለት ጽንፎች ትርጉም በአንድነት “የትም ቦታ” ማለት ንው። (See: Merism)

ከዮርዳኖስ ማዶ

“ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምዕራብ”። ሙሴ ይህንን ቃል ለእግዚአብሔር በሚናገርበት ጊዜ ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ ሞዓብ ውስጥ ነበረ።

Deuteronomy 3:26

እግዚአብሔር በእናንተ ምክንያት ተቆጥቶኝ ነበር

ይህ የሚያመለክተው ሙሴ በእስራኤል ሕዝብ ላይ በመቆጣቱ ምክንያት እግዚአብሔር እንዲያደርግ ያዘዘውን ያልታዘዘበትን ጊዜ ነው። ይህንን በዘዳግም 1፡37 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ፈስጋ

ይህንን በዘዳግም 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ዐይኖችህን አንሣ

“ዐይኖችህን አንሣ” የሚሉት ቃላት ዘይቤአዊ አነጋገር ሲሆን ተመልከት ማለት ነው። አ.ት፡ “ተመልከት” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 3:28

ቤተ ፌጎር

ይህ በፈስጋ ተራራ አጠገብ በሞዓብ ውስጥ የሚገኝ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 4

1 አሁንም እስራኤል ሆይ እንድታደርጉአቸው፥ በሕይወት እንድትኖሩና የአባቶቻችሁ አምላክ እግዚአብሔር ወደሚሰጣችሁ ምድር ሄዳችሁ እንድትወርሱ የማስተምራችሁን ሥርዓትንና ድንጋጌን ስሙ። 2 እኔ የማዛችሁን የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ትእዛዛትን ሁሉ ሳትጨምሩና ሳታጎሉ ትጠብቃላችሁ። 3 ከብዔልፌጎርም የተነሣ፥ ብዔልፌጎርን የተከተሉትን ሰዎች ሁሉ እግዚአብሔር አምላካችሁ ከመካከላችሁ እንዳጠፋ ዓይኖቻችሁ አይተወል። 4 እናንተ ግን እግዚአብሔር አምላካችሁን የተከተላችሁ እስከ ዛሬ ድረስ በሕይወት አላችሁ። 5 እነሆ እናንተ ለመውረስ በምትሄዱባቸው ምድር ሰዎች መካከል ታደርጉ ዘንድ እግዚአብሔር አምላኬ እንዳዘዘኝ ሥርዓትንና ድጋጌን አስተማርኋችሁ። 6 ስለዚህ ጠብቁአቸው፥ አድርጉአቸውም፤ ምክንያቱም ስለእነዚህ ሥርዓት ሰምተው፦ 'በእውነት ይህ ታላቅ ሕዝብ ጠቢብና አስተዋይ ሕዝብ ነው' በሚሉ ሰዎች ሁሉ ፊት ይህ ጥበባችሁና ማስተዋላችሁ ነው። 7 በምንጠራው ጊዜ ሁሉ እንደምቀርበን እንደ እግዚአሔር አምላካችን፥ ወደ እነርሱ የቀረበ አምላክ ያለው ሌላ ታላቅ ሕዝብ ማን ነው? 8 ዛሬ በፊታችሁ እንደማኖራው ሥርዓት ሁሉ ጽድቅ የሆነው ሥርዓትና ድንጋጌ ያለው ሌላ ታላቅ ሕዝብ ማን ነው? 9 ዓይኖቻችሁ ያዩትን ነገር እንዳትረሱ በሕይወታችሁም ዘመን ሁሉ ከልባችሁ እንዳይጠፋ ብቻ አስታውሉ፤በጥንቃቄም ራሳችሁን ጠብቁ። እግዚአብሔር፦ ሕዝቡን ወደ እኔ ሰብስብ በምድርም በሕይወት በሚኖሩበት ዘመን ሁሉ እኔን መፍራት ይማሩ ዘንድ ልጆቻቸውንም ያስተምሩ ዘንድ ቃሌን አሰማቸዋለሁ ብሎ እንደተናገረኝ፥ 10 በእግዚአብሔር አምላካችሁ ፊት በኮሬብ በቆማችሁ ቀን እንደሰማችሁ፥ይህን በልጆቻችሁና በልጅ ልጆቻችሁ ዘንድ እንዲታውቅ አድርጉ። 11 እናንተም ቀርባችሁ ከተራራው በታች ቆማችሁ ነበር። እስከ ሰማይም መካከል ድረስ እሳት በተራራው ላይ ይነድድ ነበር፤ ጨለማና ደመና ድቅድቅ ጨለማ ነበረ። 12 እግዚአብሔርም በእሳት ውስጥ ሆኖ ተናገራችሁ፤ ድምፅን በቃል ሰማችሁ መልክን ግን አላያችሁም፤ ድምፅን ብቻ ሰማችሁ። 13 ታደርጉትም ዘንድ ያዘዛችሁን ቃል ኪዳን አሥሪቱን ቃላት አስታወቃችሁ። በሁለቱም በድንጋይ ጽላቶች ላይ ጻፋቸው። 14 በዚያን ጊዜ ትወርሱአት ዘንድ በምትሄዱባት ምድር የምታዳርጉትን ሥርዓትና ድንጋጌ አስተምራችሁ ዘንድ እግዚአብሔር አዘዝኝ። 15 እግዚአብሔር በኮሬብ በእሳት መካከል ሆኖ በተናገራችሁ ጊዜ መልክን ከቶ እንዳላያችሁ፤ለራሳችሁ እጅግ ተጠንቀቁ። 16 የማናቸውንም ፍጥረት ምሳሌ የተቀረጸውን ምስል በወንድ ወይም በሴት፥ 17 ወይም በማናቸውም በምድር ባለው በዱር እንስሳ መልክ፥ ወይም ከሰማይም በታች የሚበርረውን የወፍን ምሳሌ፥ 18 ወይም በምድር ላይ የሚሳበውን ሁሉ ምሳሌ፥ ወይም ከምድርም በታች በውኃ ውስጥ የሚኖረውን የዓሣን ሁሉ ምሳሌ በማድረግ እንዳትረክሱ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። 19 ዓይኖቻችሁን ወደ ሰማይ አንሥታችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ ከሰማይ ሁሉ በታች ላሉት ሕዝብ ሁሉ የመደባቸውን ፀሐይንና ጨረቃን ከዋክብትንና የሰማይ ሠራዊት ሁሉ ባያችሁ ጊዜ አምልኮና ስግደት በማቅረብ እንዳትስቱ ተጠንቀቁ። 20 እናንተን ግን እግዚአብሔር እንደ ዛሬው ሁሉ የርስቱ ሕዝብ ትሆኑለት ዘንድ ወስዶ ከብረት እሳት ከግብፅ አወጣችሁ። 21 ከዚህም በተጨማሪ እግአብሔር በእናንተ ምክንያት ተቆጣኝ፣ ዮርዳኖስንም እንዳልሻገር ፥እግዚአብሔር አምላካችሁም ርስት አድርጎ ወደሚሰጣችሁ ወደመልካሚቱ ምድር እንዳልገባ ማለ። 22 እኔ ግን በዚህች ምድር እሞታለሁ፥ ዮርዳኖስንም አልሻገርም፥ እናንተ ግን ትሻገራላችሁ፥ ያችንም መልካሚቱን ምድር ትወርሳላችሁ። 23 እግዚአብሔር አምላካችሁም ከእናንተ ጋር የገባውን ቃል ኪዳን እንዳትረሱ እግዚአብሔር አምላካችሁም የከለከለውን በማናቸውም ቅርጽ የተቀረጸውን ምስል እንዳታደርጉ ተጠንቀቁ። 24 እግዚአብሔር አምላካችሁ የሚበላ እሳት ቀናተኛም አምላክ ነውና። 25 ልጆችን የልጅ ልጆችንም በወለዳችሁ ጊዜ፥ በምድሪቱም ብዙ ዘመን በተቀመጣችሁ ጊዜ፥ በማናቸውም ምስል የተቀረጸውን ምስል አድርጋችሁ በረከሳችሁም ጊዜ፥ ታስቆጡትም ዘንድ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ክፉ የሆነውን ነገር በሠራችሁ ጊዜ ትወርሱአት ዘንድ ዮርዳኖስን ተሻግራችሁ፤ 26 ከምትገቡባት ምድር እንደምትጠፉ እኔ ዛሬ ሰማይንና ምድርን በእናንተ ላይ ምስክር እንዲሆኑ እጠራለሁ፤ ዘመናችሁም አይረዝምም፥ ፈጽሞም ትጠፋላችሁም። 27 እግዚአብሔርም በአሕዛብ መካከል ይበትናችኋል፥ በአሕዛብም መካከል ጥቂት ትሆናላችሁ፥እግዚአብሔርም ያስወጣችሁኋል። 28 በዚያም የማያዩትን፥ የማይሰሙትን፥ የማይበሉትን፥ የማያሸቱትንም በሰው እጅ ከእንጨትና ከድንጋይ የተሠሩትን አማልክት ታመልካላችሁ። 29 ነገር ግን ከዚያ እግዚአብሔር አምላካችሁን ትሻላችሁ፤ በፍጹም ልባችሁ፥ በፍጹም ነፍሳችሁም የፈለጋችሁት እንደ ሆነ ታገኛላችሁ። 30 በተጨነቃችሁና ይህም ሁሉ በደርሰባችሁ ጊዜ በዘመኑ ፍጻሜ ወደ እግዚአብሔር አምላካችሁ ትመለሳላችሁ፥ ድምፁንም ትሰማላችሁ። 31 እግዚአብሔር አምላካችሁ መሓሪ አምላክ ነውና፥ አይተዋችሁም፥ አያጠፋችሁምም፤ ለአባቶቻችሁም የማለላቸውን ቃል ኪዳኑን አይረሳም። 32 እግዚአብሔር ሰውን በምድር ላይ ከፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ ከሰማይ እስከ ዳርቻዋ ድረስ ከቶ እንዲህ ያለ ታላቅ ነገር ወይም እንደ እርሱ ያለ ተሰምቶ እንደ ሆነ ከእናንተ በፊት የነበረውምን የቀደመውን ዘመን ጠይቁ። 33 እናንተ ከእሳት ውስጥ ሆኖ ሲናገር የእግዚአብሔርን ድምፅ እንደሰማችሁት ሌላ ሕዝብ ሰምቶአልን? 34 ወይም እግዚአብሔር አምላካችሁ በዓይናችሁ ፊት በግብፅ ለእናንተ እንዳደረገው ሁሉ በፈተናና በተአምራት በድንቅና በጦርነት በጸናች እጅና በተዘረጋ ክንድ በታላቅም ማስፈራት እግዚአብሔር ከሌላ ሕዝብ መካከል ለራሱ ሕዝብን ይወስድ ዘንድ በዐይናችሁ ፊት አድርጎ ያውቃልን? 35 እግዚአብሔርም አምላክ እንደ ሆነ ታውቁ ዘንድ እነዚህ ነገሮች ለእናንተ የተገለጡ ናቸው፤ከእርሱም ሌላ አምላክ የለም። 36 ያስተምራችሁ ዘንድ ከሰማይ ድምፁን አሰማችሁ፥ በምድርም ላይ ታላቁን እሳት አሳያችሁ፤ ድምፁንም ከእሳት መካከል ሰማችሁ። 37 አባቶቻችሁን ስለወደደ ከእነሱም በኋላ ዘራቸውን መረጠ፥ ከግብፅም በታላቁ ኃይል በመገኘቱ አወጣችሁ፤ 38 ዛሬ እንደ ሆነ ከእናንተ የጸኑትን ታላላቆችን አሕዛብ ከፊታችሁ ሊስያወጣቸውና ለእናንተም ምድራቸውንም ርስት አድርጎ ሊሰጣችሁ ነው። 39 እንግዲህ እግዚአብሔር በላይ በሰማይ በታችም በምድር አምላክ እንደ ሆነ፥ ሌላም እንደሌለ ዛሬ እወቁ፤ በልባችሁም ያዙት። 40 ለእናንተ ከእናንተም በኋላ ለልጆቻችሁ መልካም ይሆን ዘንድ እግዚአብሔር አምላካችሁም ለዘላለም በሚሰጣችሁ ምድር ዕድሜአችሁ ይረዝም ዘንድ እኔ ዛሬ የማዝዛችሁን ሥርዓቱንና ትእዛዙን ጠብቁ። 41 በዚያን ጊዜ ሙሴ አስቀድሞ ጠላት ያልነበረውን ሰው ሳያውቅ የገደለው ሰው 42 ወደ አንዲቱ ሸሽቶ በሕይወት ይኖር ዘንድ በምሥራቅ በኩል በዮርዳኖስ ማዶ ሦስት ከተሞች መረጠ። 43 ከተሞቹም ለሮቤል ነገድ በምድረ በዳ በደልዳላ ስፍራ ያለ ቦሶር፥ ለጋድም ነገድ በገለዓድ ያለ ራሞት፥ ለምናሴም ነገድ በባሳን ያለ ጎላን ነበሩ። 44 ሙሴ በእስራኤል ልጆች ፊት ያኖራት ሕግ ይህች ናት። 45 ሙሴና የእስራኤል ልጆች ከግብፅ ከወጡ በኋላ እግዚአብሔር የተናገራቸው የቃል ኪዳን ድንጋጌዎች፥ ሥርዓቶች፥ ሌሎችም ድንጋጌዎች እነዚህ ናቸው፤ 46 በቤተ ፌጎር አንጻር ባለው ሸለቆ፥ በሴዎን ምድር፣ ከዮርዳኖስ በስትምሥራቅ፥ በነበሩበት ጊዜ፥ሙሴና የእስራኤል ልጆች ከግብፅ በወጡበት ጊዜ ድል ያደረጉአቸው በሐሴቦን ተቀምጦ በነበረው በአራውያን ንጉሥ ነበር። 47 የእርሱንና የባሳንን ንጉሥ የዐግን ምድር ወሰዱ፤ 48 በምሥራቅ በኩል በዮርዳኖስ ማዶ የነበሩትን የሁለቱ የአሞራያን ነገሥታት እነዚህ ናቸው። ይህም ምድር ከአርኖን በአሮዔር ዳርቻ እስከ ሴዎን ተራራ እስከ አርሞንዔም ተራራ ድረስ፥ 49 በምሥራቅ በኩል የዮርዳኖስ ወንዝ ሸለቆ ሜዳ በሙሉ ጨምሮ በዮርዳኖስ ማዶ ከፈስጋ ተራራ በታች ያለውን ዓረባ ሁሉ እስከ ዓረባ ባሕር ድረስ ያለው ነው።



Deuteronomy 4:1

እኔ ላስተምራችሁ ነው

እግዚአብሔር እንዲያደርጉት የሚፈልግባቸውን ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ እየነገራቸው ነው።

እንድታደርጓቸው

“እና ታዘዟቸው”

በቃሉ ላይ አትጨምሩ -- ከእርሱም አትቀንሱ

እግዚአብሔር ሕዝቡ አዲስ ሕግ እንዲያዘጋጁ ወይም አስቀድሞ የሰጣቸውን ቸል እንዲሉ አይፈልግም።

Deuteronomy 4:3

ዐይኖቻችሁ ዐይተዋል

እዚህ ጋ “ዐይኖት” የሚያመለክቱት የእስራኤልን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “ዐይታችኋል” (See: Synecdoche)

በብዔልፌጎር ምክንያት

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በብዔልፌጎር በሠራችሁት ኃጢአት ምክንያት” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ፌጎር

ይህንን በዘዳግም 3፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

አምላካችሁ እግዚአብሔር ከመካከላችሁ አጥፍቷቸዋል

ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “የአንተ” እና “አንተ” ነጠላ ቁጥር ናቸው። (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

ከእግዚአብሔር ጋር የተጣበቃችሁ እናንተ

ጸሐፊው በእግዚአብሔር መታመንና እርሱን መታዘዝን በአካላዊ ሁኔታ አንድን ሰው ከመያዝ ጋር አመሳስሎ ይናገራል። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን ለመታዘዝ ጠንቃቆች የነበራችሁ እናንተ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:5

ተመልከቱ

“ልብ በሉ”

በምድሪቱ መካከል እንደዚሁ ልታደርጉ ይገባል

“በምድሪቱ በምትኖሩበት ጊዜ ልትታዘዟቸው ይገባችኋል”

ጠብቋቸው፣ አድርጓቸውም

በመሠረቱ ሁለቱም ሐረጎች የሚሉት ተመሳሳይ ነገር ሲሆን እንዲታዘዟቸው አጽንዖት ይሰጣል። አ.ት፡ “በጥንቃቄ ታዘዟቸው” (See: Doublet)

ይህ በሕዝቦች ፊት ጥበባችሁና ማስተዋላችሁ ነው

የነገር ስም የሆኑት “ጥበብ” እና “ማስተዋል” እንደ ቅጽል ሐረግ ሊተርጎሙ ይችላሉ፣ የነገር ስም የሆነው “ፊት” ሰዎች የአንድን ነገር ዕሴት እንዴት እንደሚፈርዱ ወይም እንደሚወስኑ ያመለክታል። አ.ት፡ “ጥበበኞችና አስፈላጊ የሆነውን የምትረዱ መሆናችሁን ለሕዝቦች የሚያሳየው ይህ ነው” (See: የነገር ስም እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ይህ ታላቅ ሕዝብ ጥበበኛና አስተዋይ ሕዝብ ነው

“መንግሥት” የሚለው ቃል ለዚያ መንግሥት ሕዝብ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የዚህ ታላቅ መንግስት ሕዝብ ጥበበኞችና አስተዋዮች ናቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:7

እንደ እርሱ ያለ ታላቅ ሕዝብ ማን አለ? ዛሬ በዚያ ማን ታላቅ ሕዝብ አለ?

እነዚህ ምላሽ የማይፈልጉ ጥያቄዎች እንደ መግለጫ ሆነው መተርጎም ይችላሉ። አ.ት፡ “እንደ እርሱ ያለ ታላቅ ሕዝብ የለም። ዛሬ ሌላ ታላቅ ሕዝብ የለም”። (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:9

ብቻ አስተውሉ -- ራሳችሁን ጠብቁ -- አትርሱ -- ዐይኖቻችሁ -- ልባችሁ -- ሕይወታችሁ -- ለልጆቻችሁና ለልጅ ልጆቻችሁ እንዲታወቁ አድርጉ -- በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት ቆማችኋል

ሙሴ እንደ አንድ ሰው አድርጎ ለእስራኤላውያን ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ”፣ “የአንተ” እና “ራሳችሁ” እንዲሁም “አስተውሉ”፣ “ጠብቁ” እና “አስታውቁ” የሚሉት ትዕዛዛት በሙሉ ነጠላ ቁጥር ናቸው። (ተውላጠ ስም እና Forms of You የሚለውን ተመልከት)

ብቻ አስተውሉ፣ ራሳችሁንም በጥንቃቄ ጠብቁ

“በጥንቃቄ አስተውሉ፣ እነዚህን ነገሮች ሁል ጊዜ ለማስታወስም እርግጠኞች ሁኑ”

አትርሱ -- ከልባችሁ አይራቁ

እነዚህ ሐረጎች የሚሉት ተመሳሳይ ነገር ሲሆን የእስራኤል ሕዝብ ያዩትን ማስታወስ እንዳለባቸው አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Parallelism)

ዐይኖቻችሁ ዐይተዋል

እዚህ ጋ “ዐይኖች” ሰውን ይወክላሉ። አ.ት፡ “ዐይታችኋል” (See: Synecdoche)

ሕዝቡን ሰብስብልኝ

“ሕዝቡን በአንድ ላይ ሰብስበህ ወደ እኔ አምጣልኝ”

Deuteronomy 4:11

ወደ ሰማይ ልብ በሚደርስ እሳት

ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። “ልብ” የአንድ ነገር “መካከል” ወይም “ውስጠኛው ክፍል” ማለት ሲሆን “ሰማይ” ደግሞ የሚያመለክተው ጠፈርን ነው። አ.ት፡ “ወደ ጠፈር በሚደርስ እሳት” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በጨለማ፣ ደመና እና ድቅድቅ ጨለማ

እዚህ ጋ “ድቅድቅ ጨለማ” የሚገልጸው ደመናን ነው። አ.ት፡ “ጥቅጥቅ ባለ ጥቁር ደመና” (See: Hendiadys)

ድቅድቅ ጨለማ

ሌላው አማራጭ ትርጉም “ከባድ ደመና” የሚለው ነው።

Deuteronomy 4:13

ዐወጀ

“እግዚአብሔር ዐወጀ”

Deuteronomy 4:15

ስለዚህ ለራሳችሁ እጅግ ተጠንቀቁ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) “ስለዚህ በምታደርጉት ነገር በጣም መጠንቀቅ ይኖርባችኋል” ወይም 2) “ነፍሳችሁን በጥንቃቄ ጠብቁ”

ራሳችሁን አታርክሱ

“ትክክል ያልሆነውን ነገር አታድርጉ”

በመሬት ላይ የሚሳብ

“በመሬት ላይ የሚጎተት”

Deuteronomy 4:19

ዐይኖችህን አንሥተህ -- ስትመለከት -- ስትቀርብ -- አምላክህ እግዚአብሔር

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት አገባቦችና “ማንሣት”፣ “መመልከት” እና “መቅረብ” ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

ለማምለክ አትቅረብ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማንም ለማምለክ እንድትፈልግ እንዲያደርግህ አትፍቀድ” ወይም “ታመልክ ዘንድ ለራስህ ፈቃድን አትስጥ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የሰማይ ሰራዊትን ሁሉ

“በጠፈር ላይ ለማየት የምትችላቸውን ነገሮች ሁሉ”። ይህ በሌላ አባባል ፀሐይን፣ ጨረቃንና ከዋክብትን ያመለክታል።

አምላክህ እግዚአብሔር ለሕዝቦች ሁሉ ከሰጣቸው ድርሻ

ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። ሙሴ፣ ምግብን እንደመሳሰሉ ትናንሽ ነገሮች እግዚአብሔር ለሕዝብ ወገኖች አከፋፍሎ እንደሚሰጣቸው የሚናገረው ስለ ከዋክብት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከብረት ምድጃ አውጥቶ አመጣችሁ

የማብሰያው ብረት እንደሚግል ሙሴ የሚናገረው ስለ ግብፅና እስራኤላውያን እንደ ብረት ሆነው በዚያ ይሠሩ ስለነበረው ከባድ ሥራ ነው። አ.ት፡ “ሰዎች ከባድ ሥራ እንድትሠሩ ከሚያደርጉበት ምድር አውጥቶ አመጣችሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የርስቱ ሕዝብ እንድትሆኑለት

ይህ “የእርሱ ብቻ የሚሆንለት ሕዝብ” ተብሎ ሊተረጎም የሚችል ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:21

በእናንተ ምክንያት እግዚአብሔር ተቆጣኝ

ሙሴ በእስራኤል ሕዝብ ላይ በመቆጣቱ ምክያንት እግዚአብሔርን ሳይታዘዝ የቀረበትን ጊዜ ያመለክታል። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። ይህንን በዘዳግም 1፡37 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

አምላክህ እግዚአብሔር ወደሚሰጥህ

ሙሴ እንደ አንድ ሰው አድርጎ ለእስራኤላውያን ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

Deuteronomy 4:23

ለራሳችሁ ተጠንቀቁ

“በጥንቃቄ አስተውሉ”

አምላክህ እግዚአብሔር የከለከለውን -- አምላክህ እግዚአብሔር

ሙሴ እንደ አንድ ሰው አድርጎ ለእስራኤላውያን ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

አምላክህ እግዚአብሔር ቀናተኛና የሚባላ እሳት ነው

ሙሴ፣ እግዚአብሔር ሲቆጣ የሚያደርጋቸውን ነገሮችን እሳት ከሚያቃጥልበት መንገድ ጋር ያነጻጽራል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሌሎች አማልክትን እንድታመልክ ስለማይፈልግ እሳት እንደሚያደርገው አምላክህ እግዚአብሔር በብርቱ ይቀጣሃል፣ ያጠፋሃልም”።(ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:25

በወለድህ -- አምላክህ እግዚአብሔር

እዚህ ጋ “አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት ቃላት ነጠላ ቁጥሮች ናቸው።

መውለድ

የአንዱ አባት ወይም አያት መሆን

ራሳችሁን ብታረክሱ

“ትክክል ያልሆነውን ብታደርጉ”። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

እርሱን ታስቆጡት ዘንድ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን ብታደርጉ

ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “እርሱ ክፉ ያለውን በማድረግ አምላካችሁን እግዚአብሔርን ታስቆጡታላችሁ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሰማይና ምድር ምስክር እንዲሆኑ እጠራቸዋለሁ

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) ሙሴ ለሚናገረው በሰማይ የሚኖሩትን ሁሉና ምድርን ምስክር አድርጎ ይጠራል ወይም 2) ሙሴ፣ ሰዎችን የሆኑ ይመስል ሰማይና ምድር እርሱ ለሚናገረው ምስክር እንዲሆኑ ይጠራቸዋል። (See: (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት and Personification)

ረጅም ዘመን አትቀመጡበትም

ረጅም ቀናት የረጅም ዕድሜ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ረጅም ዘመን መኖር አትችሉም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ነገር ግን ፈጽሞ ትጠፋላችሁ

በ4፡27 ላይ እንደተመለከተው እያንዳንዱ እስራኤላዊ አይገደልም። እዚህ ጋ “ፈጽሞ መጥፋት” በጥቅሉ ብዙ እስራኤላውያን እንደሚሞቱ አጽንዖት መስጫ ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ነገር ግን እግዚአብሔር ብዙዎቻችሁን ያጠፋችኋል” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:27

እግዚአብሔር በሕዝቦች መካከል ይበትናችኋል

ሕዝቡ ዘር የሆነ ይመስል እግዚአብሔር እርሻ ላይ እንደሚበትናቸው ሙሴ ይናገራል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ወደተለያዩ አገሮች ይላካችኋል፣ በዚያ እንድትኖሩም ያስገድዳችኋል”።(ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አርቆ ይሰዳችኋል

“ይልካችኋል” ወይም “ጠላቶቻችሁ እንዲወስዷችሁ ያደርጋል”

የሰው የእጅ ሥራ፣ እንጨትና ድንጋይ

እዚህ ጋ “የሰው እጅ” የሚያመለክተው ሰውን ራሱን ሲሆን “ሥራ -- እንጨትና ድንጋይ” ደግሞ የቀረጿቸውን ጣዖታት ያመለክታሉ። አ.ት፡ “ሰዎች የሠሯቸው የእንጨትና የድንጋይ ጣዖታት” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 4:29

ነገር ግን ከዚያ

“ነገር ግን በሌሎች አገሮች በምትኖሩበት ጊዜ”

ትፈልጉታላችሁ

እዚህ ጋ “እናንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

እርሱን በምትፈልጉበት ጊዜ

“በእርግጥ እርሱን ለመፈለግ በምትሞክሩበት ጊዜ” ወይም “እርሱን በእርግጥ ለማወቅ በምትሞክሩበት ጊዜ”

በፍጹም ልባችሁና በፍጹም ነፍሳችሁ

እዚህ ጋ “ልብ” እና “ነፍስ” የሰውን ውስጠኛ ማንነት የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። እነዚህ ሁለት ሐረጎች በአንድነት የተነገሩት “ሙሉ በሙሉ” ወይም “በቅንነት” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:30

ይመጣብሃል

“ይደርስብሃል”

በእነዚያ በኋለኞቹ ቀናት

“ከዚያ በኋላ” ወይም “ከዚያም”

ድምፁን ትሰማለህ

እዚህ ጋ “መስማት” ዘይቤአዊ አነጋገር ሲሆን ትሩሙ ማድመጥና መታዘዝ ነው። በተጨማሪም፣ “ድምፁን” የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ሆኖ እርሱ በሚናገረው ላይ አጽንዖት ይሰጣል። አ.ት፡ “እርሱ የሚላችሁን ታዘዙት” (የአነጋገር ዘይቤ እና Synecdoche የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:32

እንደ እናንተ የእግዚአብሔር ድምፅ ከእሳት መካከል ሲናገር የሰማና በሕይወት የኖረ ሕዝብ አለ?

እዚህ ጋ፣ ባለፈው ጊዜ እግዚአብሔር እንዴት አስገራሚ በሆነ መንገድ እንደተናገራቸው የእስራኤል ሕዝብ እንዲያስታውሱ ተደርገዋል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ከእናንተ በስተቀር እግዚአብሔር ከእሳት መካከል ተናግሮት በሕይወት የኖረ ሌላ ሕዝብ የለም”።(ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

የእግዚአብሔር ድምፅ ሲናገር የሰማ

እዚህ ጋ እግዚአብሔር በድምፁ ተወክሏል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሲናገር ድምፁን ሰምታችኋል” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 4:34

በጽኑ እጅና በተዘረጋች ክንድ

እዚህ ጋ “ጽኑ እጅ” እና “የተዘረጋች ክንድ” የእግዚአብሔርን ኃይል የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ጽኑ ኃይሉን በማሳየት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በዐይኖቻችሁ ፊት

እዚህ ጋ “ዐይኖች” የሚያመለክቱት የሰውን ሁለንተናውን ነው። አ.ት፡ “በፊት ለፊታችሁ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 4:35

እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ታይተዋል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እነዚህን ነገሮች አሳይቶአችኋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እንድትሰሙ አድርጓችኋል -- እንድታዩ አድርጓችኋል

“እንደሰማችሁ አረጋግጧል . . . እንዳያችሁ አረጋግጧል”

አድርጓችኋል -- ሰምታችኋል

ሙሴ ከብዙ ዓመታት በፊት በሲና ተራራ የተናገራቸውን እነዚያኑ ሕዝቦች ይናገር ይመስል ለሕዝቡ ይናገራል። በመሠረቱ በሲና ተራራ የነበሩት ሰዎች እነዚህን ቃላት ለሚናገራቸው ሰዎች አባቶቻቸው ነበሩ። አ.ት፡ “አባቶቻችሁን … አድርጓል፣ አባቶቻችሁ ሰምተዋል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:37

አባቶቻችሁ

ይህ የሚያመለክተው አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብንና የያዕቆብን ወንዶች ልጆች ነው።

በሀልዎቱ፣ በታላቅ ኃይሉ

“ከሀልዎቱ በሚመጣ በታላቅ ኃይሉ” ወይም “በታላቅ ኃይሉ”

Deuteronomy 4:39

በልብህ አኑረው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አስታውሰው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በላይ በሰማይና በታች በምድር

“በሰማይ” እና “በምድር” የሚሉት ሁለት ሐረጎች ሁለት ጽንፎችን የሚያሳዩ ሲሆኑ ትርጉማቸው “በሁሉ ስፍራ” ማለት ነው። አ.ት፡ “በሁሉ ነገር ላይ” (See: Merism)

ዕድሜህ እንዲረዝም

ረጅም ቀናት ለረጅም ሕይወት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ረጅም ዕድሜ ለመኖር እንድትችል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:41

ቦሶር -- ራሞት -- ጎላን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 4:44

ሕጉ ይህ ነው

ይህ በቀጣዮቹ ምዕራፎች ሙሴ የሚሰጣቸውን ሕግጋት ያመለክታል።

ቤተ ፌጎር

ይህ በሞዓብ ውስጥ ፈስጋ ተራራ አጠገብ የሚገኝ ከተማ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 3፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሴዎን -- አሞራውያን -- ሐሴቦን

“ንጉሥ ሴዎን … አሞራውያን ሕዝቦች … የሐሴቦን ከተማ”። እነዚህን ስሞች በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

Deuteronomy 4:47

ምድሩን

የንጉሥ ሴዎንን ምድር

የባሳን ንጉሥ ዐግ

ይህንን በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ከዮርዳኖስ ማዶ በስተምስራቅ -- ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ

ይህ ከእስራኤል በስተምስራቅ፣ ከዮርዳኖስ ወንዝ ባሻገር ያለውን ምድር ያመለክታል። ሙሴ ይህንን በሚናገርበት ጊዜ ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ ነበር። አ.ት፡ “ከዮርዳኖስ ወንዝ አቅጣጫ በስተምስራቅ … ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ በኩል”

አሮዔር

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡36 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የአርኖን ሸለቆ

ይህ የአንድ ቦታ ስም ነው። ይህንን በዘዳግም 2፡24 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሴዎን ተራራ -- የአርሞንዔም ተራራ

እነዚህ የተራራ ስሞች ናቸው። እነዚህን ስሞች በዘዳግም 3፡8-9 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

የዓረባ ባህር -- ፈስጋ ተራራ

እነዚህን ስሞች በዘዳግም 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።


Chapter 5

1 ሙሴም የእስራኤል ልጆችን ሁሉ ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦እስራኤል ሆይ፥ እንድትማሩአቸውና እንድትጠብቁአቸው ዛሬ በጆሮአችሁ የምናገራውን ሥርዓቶችንና ድንጋጌዎችን ስሙ። 2 እግዚአብሔር አምላካችን ከእኛ ጋር በኮሬብ ቃል ኪዳን አድርጎአል። 3 እግዚአብሔር ከአባቶቻችን ቃል ኪዳን አላደረገም ዛሬ በሕይወት ካለነው ከእኛ ጋር ነው። 4 እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ፊት ለፊት በተራራው ላይ በእሳት መካከል ተናገረ፥ 5 (በዚያን ጊዜ ከእሳቱም የተነሣ ፈርታችሁ ወደ ተራራው ባልቀረባችሁ ጊዜ ቃሉን ልገልጥላችሁ በእግዚአብሔርና በእናንተ መካከል ቆሜ ነበር) ። እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፦ 6 ከባርነት ቤት፥ ከግብፅ ምድር ያወጣኋችሁ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝ። 7 ከእኔ በቀር በፊቴ ሌሎች አማልክት አይኑራችሁ። 8 በላይ በሰማይ፥ወይም በታች በምድር፣ወይም ከምድርም በታች በውኃ፥ ማናቸውንም ምሳሌ የተቀረጸውን ምስል ለራሳችሁ አታድርጉ። 9 እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቀናተኛ ስለሆንኩ ለአማልክት አትስገዱላቸው፥ ወይም እነርሱን አታገልግሉአችሁ። በሚጠሉኝ ላይ እስከ ሦስተኛና አራተኛ ትውልድ ድረስ የእባቶችን ኃጢአት በልጆች ላይ ቅጣትን ያመጣል፥ 10 ለቃል ኪዳኔም ታማኝነት ለሚያሳዩኝና ለሚወዱኝ ትእዛዜንም ለሚጠብቁ እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ ምሕረትን የማደርግ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቀናተኛ አምላክ ነኝ። 11 የአምላካችሁን ስም በከንቱ አትጠቀሙ፥ እግዚአብሔር ስሙን በከንቱ የሚጠቀመውን ከበደል አያነጻውምና። 12 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንዳዘዛችሁ የሰንበትን ቀን ትቀድሱት ዘንድ ጠብቁ። 13 ስድስት ቀን ሥሩ ተግባራችሁንም ሁሉ አድርጉ፤ 14 ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ ሰንበት ነው። እናንተ እንደምታርፉ ሁሉ አገልጋያችሁና የቤት ሠራተኛችሁ ያርፉ ዘንድ እናንተ ወንድ ልጆቻችሁ፥ ሴት ልጆቻችሁም ፥ አገልጋዮቻችሁ፥ የቤት ሠራተኞቻችሁም በፊታችሁ፥ አህዮቻችሁም፥ ከብቶቻችሁም፥ ሁሉ በደጆቻችሁ ውስጥ ያለው እንግዳም ጭምር በሰንበት ምንም ሥራ አትሥሩ። 15 እናንተም በግብፅ በሪያ እንደ ነበራችሁ አስቡ፥ እብዚአብሔር አምላካችሁ በጸናች እጅና በተዘረጋች ክንድ ከዚያ አውጣችሁ። ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችሁ የሰንበትን ቀን ትጠብቁ ዘንድ አዘዛችሁ። 16 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንዳዘዛችሁ ፤ እግዚአብሔር አምላካችሁ በሰጣችሁ ምድር ላይ ዕድሜአችሁ እንዲረዝምና መልካም እንዲሆንላችሁ አባታቸውንና እናታቸውን አክብሩ። 17 አትግደሉ። 18 አታመንዝሩ። 19 አትስረቁ። 20 በባልንጀራችሁ ላይ በሐሰት አትመስክሩ። 21 የባልንጀራችሁን ሚስት አትመኙ፤ የባልጀራችሁን ቤት፥ እርሻውንም፥ አገልጋዩንም፥ የባልጀራችሁንም በሬውንም፥ አህያውንም፥ ከባልጀራችሁ ገንዘብ ሁሉ ማናቸውንም አትመኙ። 22 እግዚአብሔር በተራራው ላይ በእሳትና በደመና በጨለማም ውስጥ ሆኖ በታላቅ ድምፅ፥ እነዚህን ቃሎች ለጉባኤአችሁ ሁሉ ከተናገረው ምንም አልጨመረም። በሁለቱም የድንጋይ ጽላችቶች ላይ ጻፋቸው ለእኔም ሰጠኝ። 23 ተራራው በእሳት ሲነድድ ከጨለማው ውስጥ ድምፁን በሰማችሁ ጊዜ እናንተ የነገዶቻችሁ አለቆች ሽማግሌዎቻችሁም ወደ እኔ ቀረባችሁ። 24 አላችሁም፦ እነሆ አምላካችን እግዚአብሔር ክብሩንና ታላቅነቱን አሳይቶናል፥ ከእሳትም ውስጥ ድምፁን ሰምተናል፤ እግዚአብሔርም ከሰዎች ጋር ሲነጋገር ሰዎችም በሕይወት ሲኖር ዛሬ አይተናል። 25 አሁን እንግዲህ ይህች ታላቂቱ እሳት ታቃጥለናለችና ለምን እንሞታለን? እኛ የእግዚአብሔርን የአምላካችንን ድምፅ ደግሞ ብንሰማ እንሞታለን። 26 ከሥጋ ለባሽ ሁሉ እኛ እንደ ሰማን በእሳት ውስጥ ሆኖ ሲናገር የሕያው አምላክን ድምፅ ሰምቶ በሕይወቱ የኖረ ማን ንው? 27 አንተ ቅረብ፤ እግዚአብሔር አምላካችን የሚለውን ሁሉ ስማ፤ እግዚአብሔር አምላካችንም ለአንተ የሚናገረውን ሁሉ ለእኛ ንገረን፤ እኛም ሰምተን እናደርገዋለን አላችሁ። 28 በተናገራችሁኝም ጊዜ እግዚአብሔር የእናንተን ቃል ሰማ። እግዚአብሔርም አለኝ፦ይህ ሕዝብ የተናገሩህን ቃል ሰምቼአለሁ፤ የተናገሩትም ሁሉ መልካም ነው። 29 ለእነርሱ ለዘላለምም ለልጆቻቸው መልካም ይሆንላቸው ዘንድ፥ እንዲፈሩኝ፥ ሁልጊዜም ትእዘዜን ሁሉ እንዲጠብቁ፥ እንዲህ ያለ ልብ ምነው በነበራቸው! 30 ሄደህ እንዲህ በላቸው፦ ወደ ድንኳናችሁ ተመለሱ። 31 አንተ ግን በዚህ በእኔ ዘንድ ቁሙ፥ ርስት አድርጌ በምሰጣቸውም ምድር ላይ ያደርጉአት ዘንድ የምታስተምራቸውን ትእዛዜንና ሥርዓቴን፥ ድንጋጌንም ሁሉ እነግርሃለሁ። 32 ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችሁ እንዳዘዛችሁ ታደርጉ ዘንድ ጠብቁ፥ ከእርሱም ወደ ቀኝም ወደ ግራም ፈቀቅ አትበሉ። 33 በሕይወት እንድትኖሩ መልካምም እንዲሆንላችሁ፥ በምትወርሱአትም ምድር ዕድሜአችሁ እንዲረዝም፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ ባዘዛችሁ መንገድ ሁሉ ሄዱ።



Deuteronomy 5:1

እስራኤልን ሁሉ ጠራ

እዚህ ጋ “ሁሉ” የሚለው ቃል ግነት ነው። ሙሴ በእስራኤል ያሉ ሁሉ ቃሉን እንዲሰሙና እንዲታዘዙ ፈልጓል፣ ይሁን እንጂ ሁሉ ይሰማው ዘንድ ምናልባት ድምፁ በጣም ከፍ ያለ አልነበረም። (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

ዛሬ በጆሮአችሁ የምናገረውን

እዚህ ጋ “ጆሮ” የሚያመለክተው የሰውን ሁለንተናውን ነው። ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር አጽንዖት የሚሰጠው ሰዎቹ ኃጢአትን እንዳያደርጉ ሙሴ የነገራቸውን እንደሚያውቁና ኃጢአት መሥራታቸውን አለማወቃቸውን እንዳይናገሩ ነው። አ.ት፡ “ዛሬ የምነግራችሁን” (Synecdoche እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር ከአባቶቻችን ጋር ይህንን ቃል ኪዳን አላደረግም

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ያደረገው ከኋለኛው የእስራኤል ትውልድ ጋር ደግሞ እንጂ በኮሬብ ከነበሩት ጋር ብቻ አይደለም ወይም 2) እግዚአብሔር በሩቅ ከነበሩት አባቶቻቸው አብርሃምን፣ ይስሐቅንና ያዕቆብን ከመሳሰሉት ጋር ይህንን ቃል ኪዳን አላደረገም፤ ይልቁንም ይህ ቃል ኪዳን የጀመረው በኮሬብ ከነበሩት እስራኤላውያን ጋር ነው።

Deuteronomy 5:4

ፊት ለፊት

ለእርስ በርሳቸው ቅርበት ያላቸው ሁለት ሰዎች ሲነጋገሩ እርስ በርስ እንደሚተያዩ ለመግለጽ የቋንቋህን የአነጋገር ዘይቤ ተጠቀም። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 5:7

በፊቴ ሌሎች አማልክት አይኑሩህ

“እኔን እንጂ ሌሎች አማልክትን ማምለክ የለብህም”

ከምድር በታች ያለውን ወይም ከውሃ በታች ያለውን

ይህ በይበልጥ ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከእግሮቻችሁ በታች ባለው ምድር ላይ ያለ ወይም ከምድር በታች በውሃ ውስጥ ያለ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 5:9

አትስገዱላቸው ወይም አታገልግሏቸው

“የተቀረጹትን ምስሎች አታምልኩ ወይም እነርሱ የሚያዟችሁን አታድርጉ”

አታድርግ

“መቼም ቢሆን”

እኔ ቀናተኛ አምላክ ነኝ

“እኔን ብቻ እንድታመልኩኝ እፈልጋለሁ”

ለሚወዱኝ የቃል ኪዳን ታማኝነቴን ለሺዎች የማሳይ

“ታማኝነት” የሚለው የነገር ስም “በታማኝነት” ወይም “ታማኝ” ተብሎ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሚወዱኝን ሺዎችን በታማኝነት እወዳቸዋለሁ” ወይም “ከሚወዱኝ ከሺዎች ጋር ለቃል ኪዳን ታማኝ እሆናለሁ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ለሚወዱኝ ለሺዎች

አንዳንድ ትርጓሜዎች “ለሚወዱኝ ለአንድ ሺህ ትውልዶች” በሚል ይነበባሉ። “ሺዎች” የሚለው ቃል ለመቁጠር የሚበዛውን ቁጥር ለማመልከት የሚውል ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ለሚወዱኝ ለእነርሱ እስከ ዘላለም” (Assumed Knowledge and Implicit Information፣ ፈሊጣዊ አነጋገር እና ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 5:11

የእግዚአብሔርን ስም አታንሣ

“በእግዚአብሔር ስም አትጠቀም”

አታድርግ

ይህንን በዘዳግም 5፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

በከንቱ

“በግድየለሽነት” ወይም “ተገቢውን አክብሮት ባለመስጠት” ወይም “ለተሳሳቱ ዓላማዎች”

እግዚአብሔር ከበደል አያነጻውም

ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በደለኛ አድርጎ ይቆጥረዋል” ወይም “እግዚአብሔር ይቀጣዋል” (ድርብ አሉታዎች የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 5:12

ቅዱስ አድርገህ እንድትጠብቀው

“ለእግዚአብሔር እንድትለየው”

ሥራህን ሁሉ ሥራ

“የተለመደውን ሥራህን ሁሉ ሥራ”

ሰባተኛው ቀን

“ቀን 7”። እዚህ ጋ “ሰባተኛው” ለሰባት ተራ ቁጥር ነው። (See: Ordinal Numbers)

በእርሱ አትሥራበት

“በዚያን ቀን ምንም አትሥራ”

በደጆችህ ውስጥ

እዚህ ጋ “ደጆች” ከተማን ራሱን የሚያመላክት ነው። አ.ት፡ “በማኅበረሰብህ መካከል” ወይም “በከተማህ ውስጥ” ወይም “ከአንተ ጋር የሚኖሩ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 5:15

አስታውስ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ማስታወስ አለብህ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በጽኑ እጅና በተዘረጋች ክንድ

እዚህ ጋ “ጽኑ እጅ” እና “የተዘረጋች ክንድ” የእግዚአብሔርን ኃይል የሚያሳይ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡34 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ጽኑ ኃይሉን በማሳየት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 5:17

አታድርግ

ይህንን በዘዳግም 5፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

አታመንዝር

“ከሚስትህ በቀር ከሌላ ከማንም ጋር አትተኛ”

በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር

“ስለ ሌላው ሰው ውሸትን አትናገር”

Deuteronomy 5:21

አታድርግ

ይህንን በዘዳግም 5፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 5:23

ድምፁን ሰምታችኋል

“ድምፅ” የሚለው ቃል የቃልን ድምፅ ወይም ተናጋሪውን ሰው የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የቃሉን ድምፅ ሰምታችኋል” ወይም “እግዚአብሔር ሲናገር ሰምታችኋል” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 5:25

ታዲያ ለምን እንሞታለን?

እግዚአብሔር ከተናገራቸው እንደሚሞቱ በማሰብ ፈርተው ነበር። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እንሞታለን ብለን ፈርተናል” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ያደረገ -- ከእኛ በቀር ማን አለ?

ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “… ያደረገ ከእኛ በቀር ሌላ አንድም ሕዝብ የለም”። (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ሥጋ ሁሉ

ይህ ሰዎችን ሁሉ ወይም ሕያዋን ፍጥረታትን ይወክላል። አ.ት፡ “ሰዎች ሁሉ” ወይም “ሕያዋን ፍጥረታት በሙሉ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 5:28

በነገራችሁኝ ጊዜ

እዚህ ጋ “እኔን” የሚያመለክተው ሙሴን ነው።

ምነው በኖራቸው

የአንተ ቋንቋ ለአንድ ነገር የሞኖርን ብርቱ ፍላጎት የሚገልጽ የአነጋገር ዘይቤ ካለው እዚህ ጋ ልትጠቀምበት ያስፈልግህ ይሆናል። አ.ት፡ “ቢኖሩ በጣም ደስ ይለኝ ነበር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 5:31

ታስተምራቸዋለሁ

“የእስራኤልን ሕዝብ ታስተምራለህ”

Deuteronomy 5:32

ጠብቁ

ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ ትዕዛዝ እየሰጠ ነው።

ወደ ቀኝም ወደ ግራም አትበሉ

ይህ እግዚአብሔርን የማይታዘዘውን ሰው ከትክክለኛው መንገድ ከሚወጣው ሰው ጋር ያነጻጽረዋል። አ.ት፡ “በየትኛውም መንገድ ለእርሱ የማትታዘዝ መሆን የለብህም” ወይም “የሚላችሁን ሁሉ ማድረግ አለባችሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዕድሜአችሁ እንዲረዝም

ረጅም ቀናት የረጅም ዕድሜ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። ይህንን በዘዳግም 4፡40 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ረጅም ዕድሜ መኖር እንድትችሉ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 6

1 ከዮርዳኖስ ማዶ በምትውርሱአት ምድር የምትጠብቃችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ እንዳስተምራችሁ ያዘዘኝ እነዚህ ትእዛዘት፥ ሥርዓትና ድንጋጌዎች እነዚህ ናቸው፤ 2 እኔ የማዛችሁን ሥርዓትንና ትእዛዘትን በመጠበቅ እናንተ፥ ልጆቻችሁ፥ የልጅ ልጆቻችሁም በዘመናችሁ ዕድሜአችሁ እንዲረዝም እግዚአብሔር አምላካችሁን አክብሩ። 3 እንግዲህ እስራኤል ሆይ፥ ስማ፤ መልካምም እንዲሆንላችሁ የአባቶቻችሁም አምላክ እግዚአብሔር ተስፋ እንደሰጣችሁ ወተትና ማር በምታፈስሰው ምድር እጅግ እንድትበዙ ነው። 4 እስራኤል ሆይ፥ ስማ፥ እግዚአብሔር አምላካችን አንድ እግዚአብሔር ነው። 5 እናንተም እግዚአብሔር አምላካችሁን በፍጹም ልባችሁ፥ በፍጹም ነፍሳችሁ፥ በፍጹም ኃይላችሁ ውደዱ። 6 እኔም ዛሬ እናንተን የማዝዘው ቃል በልባችሁ ይሁን፤ 7 በቤታችሁም ስትቀመጡ፥ በመንገድም ስትሄዱ፥ ስትተኙም፥ ስትነሡም፥ ልጆቻችሁን አስተምሩአቸው። 8 በእጃችሁም ምልክት አድርጋችሁ እሰሩት፥ በዓይኖቻችሁም መካከል እንደክታብ ይሁንላችሁ። 9 በቤታችሁም መቃኖች በደጃፋችሁም በሮች ላይ ጻፉት። 10 እግዚአብሔር አምላካችሁ ለእናንተ ሊሰጣችሁ ለአባቶቻችሁ ለአብርሃም፥ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ወደ ማለላቸው ምድር ባገባችሁ ጊዜ፥ ያልሠራሃችኋቸውን ታላላቅና መልካም ከተሞች፥ 11 በመልካም ነገሮች ሁሉ የተሞሉ ቤቶች ያልማስሃችኋቸውን የተማሱ ጉድጓዶች፥ ያልተከልሃችኋቸውን ወይንና ወይራ በሰጣችሁ ጊዜ፥ 12 በበላችሁና በጠገባችሁ ጊዜ፥ በዚያን ጊዜ ከግብፅ ምድር ከባርነት ቤት ያወጣችሁን እግዚአብሔርን እንዳትረሱ ተጠንቀቁ። 13 አምላካችሁን እግዚአብሔርን አክብሩ፤ እርሱንም አምልኩት በስሙም ማሉ። 14 በዙሪያችሁ ያሉትን አሕዛብ የሚያመልኩአቸውን ሌሎችን አማልክት ፍለጋ እንዳትሄዱ፥ እንዳከተከተሉ፤ 15 ምክንያቱም በመካከላችሁ ያለው እግዚአብሔር አምላካችሁ ቀናተኛ አምላክ ስለሆነ፥ ቁጣው እንዳይነድባችሁና ከምድር ገጽ እንዳያጠፋችሁ ተጠንቀቁ። 16 በማሳህ እንደተፈታተናችሁት እግዚአብሔር አምላካችሁን አትፈታተኑት። 17 ያዘዝኋችሁን የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ትእዛዘትንና ሥርዓቱን አጥብቃችሁ ጠይቁ። 18 መልካምም ይሆንላችሁ ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ቅኑንና መልካሙን ነገር አድርጉ፤ እግዚአብሔርም ለአባቶቻችሁ ወደ ማለላቸው ወደ መልካሚቱ ምድር ገብታችሁ እንድትወርሱ፥ 19 እግዚአብሔርም እንደተናገረ ጠላቶቻችሁን ሁሉ ከፊታችሁ ያወጣላችሁ ዘንድ። 20 በኋለኛው ዘመንም ልጆቻችሁ እንዲህ ብለው በጠየቃችሁ ጊዜ፦ እግዚአብሔር አምላካችን ያዘዛችሁ የቃል ኪዳን ድንጋጌዎች፥ ሥርዓትና ሌሎችስ ድንጋጌዎች እነዚህ ምንድን ናቸው? 21 እናንተም ለልጆቻችሁ እንዲህ በሉአችው፦ በግብፅ አገር የንጉሥ ፈርዖን አገልጋዮች ነበርን፥ እግዚአብሔርም በጽኑ እጅ ከግብፅ አወጣን፥ 22 እግዚብብሔርም በግብፅና በፈርዖን፥ በቤቱም ሁሉ ላይ በዓይናችን ፊት ታላቅና ክፉ፥ ምልክትና ተአምራትን አደረገ። 23 ለአባቶቻችን ወደ ማለላቸው ምድር አምጥቶን እርስዋን ይሰጠን ዘንድ ከዚያ አወጣን። 24 እንደ ዛሬም በሕይወት እንዲያኖረን ሁልጊዜም መልካም እንዲሆንልን እግዚአብሔር አምላካችንን እንፈራ ዘንድ ይህችንም ሥርዓት ሁሉ እናደርግ ዘንድ እግዚአብሔር አዘዘን። 25 እርሱም እንዳዘዘን በእግዚአብሔር በአምላካችን ፊት እንፈጽመው ዘንድ ይህን ትእዛዝ ሁሉ ብንጠብቅ ለእኛ ጽድቅ ይሆንልናል።



Deuteronomy 6:1

ትጠብቁት ዘንድ -- ለመጠበቅ

“ትታዘዙ ዘንድ … ለመታዘዝ”

ዮርዳኖስን ተሻግራችሁ

“ከዮርዳኖስ ወንዝ ወዲያ ማዶ ሄዳችሁ”

ዕድሜአችሁ እንዲረዝም

ረጅም ቀናት የረጅም ዕድሜ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህ በዘዳግም 4፡26 እንዳለው በተመሳሳይ “ረጅም ዘመን እንድትኖሩ” ተብሎ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ዕድሜአችሁን እንዳረዝመው” ወይም “ረጅም ዕድሜ እንድትኖሩ አደርጋችሁ ዘንድ” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 6:3

እነርሱን ስማ

እዚህ ጋ “ስማ” ማለት ታዘዝ ሲሆን “እነርሱን” የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት፣ ሕግጋትና ሥርዓት ስማ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information

ጠብቃቸው

“ታዘዛቸው”

ወተትና ማር የምታፈሰውን ምድር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “የተትረፈረፈ ወተትና ማር የሚፈስባት ምድር” ወይም “ከብት ለማርባትና ለእርሻ ምርጥ የሆነ ምድር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 6:4

አምላካችን እግዚአብሔር አንድ ነው

“አምላካችን እግዚአብሔር አንድና ብቸኛ አምላክ ነው”

በሙሉ ልብህ፣ በሙሉ ነፍስህና በሙሉ ኃይልህ

እዚህ ጋ “ልብ” እና “ነፍስ” የአንድን ሰው ውስጣዊ ማንነት የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። እነዚህ ሦስቱ ሐረጎች በአንድነት ጥቅም ላይ የዋሉት “በፍጹም” ወይም “በቅንነት” ለማለት ነው። በዘዳግም 4፡29 ላይ “በሙሉ ልብህ፣ በሙሉ ነፍስህ” የሚለውን እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 6:6

እኔ የማዝህን

ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ የሚናገረው የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ነው።

በልብህ ይኑር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ሁል ጊዜ ማስታወስ አለብህ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በትጋት አስተምረው -- ተናገረው

“በትጋት እንድታስተምረው አዝሃለሁ … እንድትናገረው አዝሃለሁ”። አንባቢው እነዚህን እንደ ትዕዛዝ ሊረዳቸው ይገባዋል።

Deuteronomy 6:8

እሰራቸው

ይህ “እነዚህን ቃላት በብራና ላይ ጻፋቸው፣ ብራናውን በትንሽ ኪስ ውስጥ አድርገውና ኪሱን እሰረው” ለሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር በተራው “በአካል እዚያ ያሉ ያህል እነዚህን ቃሎች ታዘዛቸው” ለሚለው ዘይቤአዊ አነጋገር ሊሆን ይችላል። አ.ት፡ “እነዚህን ቃላት እሰራቸው”። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእጅህ ላይ እንደ ምልክት

“ሕጌን እንድታስታውስ እንደሚያደርግህ አንዳች ነገር”

እንደ ግንባር ጌጥ ያገለግሉሃል

ይህ “እነዚህን ቃላት በብራና ላይ ጻፋቸው፣ ብራናውን በትንሽ ኪስ ውስጥ አድርገውና በዚያ እንዲቀመጥ ትንሹን ኪስ በግምባርህ ላይ እሰረው” ለሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር በተራው “በአካል እዚያ ያሉ ያህል እነዚህን ቃሎች ታዘዛቸው” ለሚለው ዘይቤአዊ አነጋገር ሊሆን ይችላል። አ.ት፡ “ቃሎቼ እንደ ግምባር ጌጥ ያገለግላሉ”። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ክታብ

አንድ ሰው በግምባሩ ላይ የሚያደርጋቸው ጌጣ ጌጦች

ጻፍ

ይህ ትዕዛዝ ነው።

Deuteronomy 6:10

አንተ ያልሠራኻቸውን ሰፋፊና በጣም ያማሩ ከተሞች

የከነዓንን ሕዝቦች በሚያሸንፉበት ጊዜ እነዚህ ከተሞች በሙሉ የእስራኤል ሕዝብ ይሆናሉ።

ከባርነት ቤት ያወጣህ

እዚህ ጋ “የባርነት ቤት” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው እስራኤላውያን ባሪያዎች የነበሩበትን ስፍራ፣ ግብፅን ነው። አ.ት፡ “ባሪያ ሆነህ ከኖርክበት ስፍራ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 6:13

አምላክህን እግዚአብሔርን ታከብራለህ፤ እርሱንም ታመልካለህ፣ በእርሱም ስም ትምላለህ

“ማክበር የሚኖርብህ አምላክህን እግዚአብሔርን እንጂ ሌላውን አይደለም፤ ማምለክ ያለብህ እርሱን ብቻ ነው፣ መማል የሚኖርብህም በእርሱ ስምና በእርሱ ስም ብቻ ነው”። እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ሌሎች አማልክቶችን እንዳያመልኩ ወይም እንዳያገለግሉ ስለመናገሩ ምናልባት የአንተ ቋንቋ አጽንዖት የሚሰጥበት ሌላ መንገድ ይኖር ይሆናል።

በስሙ ትምላለህ

በእግዚአብሔር ስም መማል ማለት እግዚአብሔርን የመሓላው መሠረት ወይም ኃይል ማድረግ ማለት ነው። “በስሙ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ራሱን ነው። አ.ት፡ “ትምላለህ፣ እግዚአብሔር እንዲያጸናውም ትጠይቃለህ” ወይም “በምትምልበት ጊዜ ስሙን ትጠራለህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በመካከልህ

“በመካከልህ የሚኖር”

የአምላክህ የእግዚአብሔር ቁጣ በአንተ ላይ ይነዳል

ሙሴ የእግዚአብሔርን ቁጣ አንድን ነገር ለማቃጠል እሳት ከሚለኩስ ሰው ጋር ያነጻጽረዋል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ቁጣን መለኮስ በጣም የመቆጣት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር ቁጣውን ያነዳል” ወይም “አምላክህ እግዚአብሔር በጣም ይቆጣል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከ -- ያጠፋሃል

“ምንህም እስከማይተርፍ ድረስ ያጠፋሃል”

Deuteronomy 6:16

እግዚአብሔርን አትፈታተነው

እዚህ ጋ “መፈተን” ማለት እግዚአብሔርን መገዳደርና ትክክለኛ መሆኑን እንዲያረጋግጥ ማስገደድ ማለት ነው።

ማሳህ

ይህ በምድረ በዳው ውስጥ ያለ የቦታ ስም ነው። ተርጓሚው ምናልባት፣ “’ማሳህ’ የሚለው ስም ትርጉም ‘መፈተን’ ማለት ነው” የሚል የግርጌ ማስታወሻ መጨመር ይኖርበት ይሆናል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 6:18

በእግዚአብሔር ፊት ትክክለኛና መልካም የሆነውን አድርግ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ትዕዛዝና በረከት ነው። እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ከታዘዙት ከእርሱ በረከትን ይቀበላሉ። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ትክክልና መልካም የሚለውን አድርግ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 6:20

ያዘዛችሁ የቃል ኪዳኑ ድንጋጌዎች ምንድናቸው

በዚህ ጥያቄ “የቃል ኪዳን ድንጋጌዎች” ትርጉማቸውንና ዓላማቸውን ይወክላሉ። አ.ት፡ “የታዘዙት የቃል ኪዳን ድንጋጌዎች ለአንተ ምን ትርጉም አላቸው” ወይም “የታዘዝከውን የቃል ኪዳን ድንጋጌዎች መታዘዝ የሚኖርብህ ለምንድነው”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ልጅህ

ይህ የሚያመለክተው ሙሴ የእግዚአብሔርን ቃል የሚነግራቸው የትልልቆቹ እስራኤላውያንን ልጆች ነው።

በጽኑ እጅ

እዚህ ጋ “ጽኑ እጅ” የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ኃይል ነው። ይህንን በዘዳግም 4፡34 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት፡ አ.ት፡ “በጽኑ ኃይሉ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በቤቱ ሁሉ

እዚህ ጋ “ቤቱ” የሚለው ፈሊጣቂ አነጋገር የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “በሕዝቡ ሁሉ ላይ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በዐይኖቻችን ፊት

እዚህ ጋ “ዐይኖቻችን” የሚለው ቃል የሚያመለክተው የሰውን ሁለንተናውን ነው። አ.ት፡ “ልናያቸው በምንችልበት” (See: Synecdoche)

ሊያስገባን

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም መብራራት ይችላል። አ.ት፡ “ወደ ከነዓን ሊያስገባን” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 6:24

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ሀልዎች” ወይም “እግዚአብሔር ሊያየን በሚችልበት”

ጠብቅ

ሁል ጊዜ፣ በየትኛውም ሁኔታ ታዘዝ

ይህ ጽድቃችን ይሆናል

“ይህ” የሚለው ቃል የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት መጠበቅን ያመለክታል። ይህ እግዚአብሔር ጻድቅ አድርጎ እንደሚቆጥራቸው የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ጻድቅ አድርጎ ይቆጥረናል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 7

1 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንድትወሱአት ወደምትገቡባት ምድር ባመጣችሁ ጊዜ፤ ከፊታችሁም ብዙ አሕዛብ ከእናንተ የበለጡትንና የበረቱትን ሰባቱን አሕዛብ ኬጢያዊውን፥ ጌርጌሳውያንን፥ አሞራውያንብ፥ ከነዓናውያንን፥ፌርዛዊውን፥ ኤዊያዊውንና ኢያቡሳዊውን አወጣቸው። 2 እንዲሁም ጦርነት በገጠማችሁ ጊዜ እግዚአብሔር አምላካችሁ ድል በሰጣችሁ ጊዜ፥ እነርሱን ማጥቃት አለባችሁ፥ ከዚያም ፈጽሞ ማጥፋት ይኖርባችኋል። 3 ከእርሱም ጋር ቃል ኪዳን ማድረግ ወይም ምሕረት አለማድረግ፥ ከእነርሱም ጋር አትጋቡም፤ ሴት ልጆቻችሁን ለወንድ ልጆቻቸው አትስጡ፥ ሴት ልጃቸውንም ለወንድ ልጃችሁ አትውሰዱ። 4 ሌሎች አማልክትን እንዳያመልኩ፥ ልጆቻችሁን እኔን እንዳይከተሉ ይመልሳሉ፥ የእግዚአብሔርም ቁጣ ይነድድባችኋል ፈጥኖም ያጠፋችኋል። 5 በእነርሱ ላይ የምታደርጉባቸው እንደዚህ ነው፥ መሠዊያቸውን አፍርሱ፥ ሐውልቶቻቸውንም ሰባብሩ፤ የማምለኪያ ዐፀዶቻቸውንም ቁረጡ፥ የተቀረጸውን ምስላቸውንም በእሳት አቃጥሉ። 6 እናንተ ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ የተለያችሁ ሕዝብ ናችሁ። እግዚአብሔር አምላካችሁ በምድርም ገጽ ከሚኖሩ ሕዛብ ሁሉ ይልቅ ለእርሱ ሕዝብ ትሆንለት ዘንድ መረጣችሁ። 7 እግዚአብሔርም የወደዳችሁና የመረጣችሁ ከአሕዛብ ሁሉ በቁጥር ስለ ባዛችሁ አይደለም፤ እናንተ ከአሕዛብ ሁሉ በቁጥር ጥቂቶች ነበራችሁና፤ 8 ነገር ግን እግዚአብሔር ስለ ወደዳችሁ ለአባቶቻችሁም የማለላቸውን ቃል ኪዳን ስለ ጠበቀ ነው። እግዚአብሕር በጽኑ እጅ ያወጣችሁ፥ ከባሪነትም ቤት ከግብፅ ንጉሥ ከፈርዖን እጅ ያዳናችሁ ለዚህ ነው። 9 ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችሁ እርሱ አምላክ እንደ ሆነ ለሚወድዱትና ትእዛዘትንም ለሚጠብቁት፥ ቃል ኪዳኑንና ምሕረቱን እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ የሚጠብቅ የታመነ አምላክ እንደ ሆን እወቁ፥ 10 ነገር ግን የሚጠሉትን በፊታቸው ሊያጠፋቸው ብድራትን ይመልሳል፤እንዲሁም ብድራትን ለመመለስ አይዘገይም። 11 እንግዲህ ታደርጉት ዘንድ እኔ ዛሬ ለእናንተ የማዝዘውን ትእዛዘት፥ ሥርዓቶችና ድንጋጌዎችን ጠብቁ። 12 እነዚህን ድንጋጌዎችን ሰምታችሁ ብትጠብቁና ብታደርጉ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ ለአባቶቻችሁ የማለላችውን ቃል ኪዳን በታማኝነት ለእናንተ ይጠብቅላችኋል። 13 እርሱም ይወድዳችኋል፥ ይባርካችኋል፥ ያበዛላችኋል፤ እንዲሁም የሆዳችሁንና የምድራችሁን ፍሬ፥ እህላችሁን፥ ወይናችሁን፥ ዘይታችሁን፥ የከብቶቻችሁንና የበጎቻችሁን መንጋ ይባርካል። 14 ከአሕዛብም ሁሉ ይልቅ የተባረካችሁ ትሆናላችሁ፥ በሰዎቻችሁና በከብቶቻችሁ ዘንድ ወንድ ወይም ሴት ቢሆኑ መካን አይሆንባችሁም። 15 እግዚአብሔርም ሕመምን ሁሉ ከእናንተ ያርቃል፥ የምታውቁአችሁን ክፉውን የግብፅ በሽታ ሁሉ በእናንተ ላይ አያደርስባችሁም በሚጠሉባችሁም ሁሉ ላይ ያመጣባቸዋል። 16 እግዚአብሔር አምላካችሁም በእጃችሁ አሳልፎ የሚሰጣችሁን አሕዛብ ሁሉ ታጠፋቸዋላችሁ፥ ዓይናችሁም አያዝኑላቸውም። ወጥመድ እንዳይሆኑባችሁአማልክታቸውንም አታምልኩአችሁም። 17 በልብህም እንዲህ ብትሉ፦ እነዚህ አሕዛብ ከእኔ ይልቅ ይበዛሉና አወጣቸው ዘንድ እንዴት እችላለሁ? 18 እግዚአብሔር አምላካችሁ በፈዖንና በግብፅ ሁሉ ያደረገውን ትዝ ስለሚላችሁ እነሱን አትፍራቸው፤ 19 አምላካችሁ እግዚአብሔር ዓይናችሁ ፊት ታላቅን መቅሠፍት፥ ምልክትንና ተአምራትን በማድረግ በጸናችው እጅ፥ በተዘረጋውም ክንድ አወጣችሁ። እንዲሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ እናንተ በምትፈሩአችሁ በአሕዛብ ሁሉ ላይ ያደርጋል። 20 በተጨማሪም እግዚአብሔር አምላካችሁ ራሳቸውን የተሸሸጉትን ከፊታችሁ እስኪጠፉ ድረስ በመካከላችው ተርብ ይሰድድባቸዋል። 21 እግዚአብሔር አምላካችሁ ታላቅና የተፈራ አምላክ በመካከላችሁ ስላለ፤ ከእነርሱ የተነሣ አትደንግጡ። 22 እግዚአብሔር አምላካችሁ እነዚህን አሕዛብ ጥቂት በጥቂት ከፊታችሁ ያወጣቸዋል። ሁሉንም አንድ ጊዜ አታጠፋቸውም፤ ወይም የዱር አራዊት በዙሪያችሁ በጣም ብዙ ይሆናሉ። 23 እግዚአብሔር አምላካችሁ እነርሱን በእጃችሁ አሳልፎ ይሰጣቸዋል፥ እስኪጠፉም ድረስ በታላቅ ድንጋጤ ያስደነግጣቸዋል። 24 ነገሥታታቸውንም በእጃችሁ አሳልፎ ይሰጣቸዋል፥ ስማቸውንም ከሰማይ በታች ታጠፋቸዋላችሁ። እስክታጠፏቸውም ድረስ ማንም በፊታችሁ ይቆም ዘንድ አይችልም። 25 የተቀረጸውንም የአማልክታቸውን ምስል በእሳት ታቃጥላላችሁ፤ ከብር ወይም ከወርቅ የተሠሩትንም ለራሳችሁ ለመውሰድ አትመኙ፥ በእግዚአብሔር በአምላካችሁም ዘንድ ርኩስ ነውና እንዳትጠመዱበት ከእርሱ ምንም አትውሰዱ። 26 እንደ እርሱም ርጉም እንዳትሆኑ ርኩስን ነገር ወደ ቤታችሁ አታግቡ ለማምለክም አትቃጡ፥ ለጥፋት የተለየ ስለ ሆነ ፈጽሞ ተጸየፉት፥ ጥሉትም።



Deuteronomy 7:2

አሳልፎ ይሰጥሃል

አንድ ሰው ለሌላው እንደሚሰጠው ቁሳዊ ነገር ሙሴ የሚናገረው ስለ ድል ነው። አ.ት፡ “እንድታሸንፋቸው ያስችልሃል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስታሸንፋቸው

እዚህ ጋ “እነርሱን” የሚያመለክተው በዘዳግም 7፡1 የተጠቀሱትን ሰባት አገሮች ነው።

Deuteronomy 7:4

እነርሱ

“ልጆችህ ከሌሎች አገሮች ሕዝቦች ጋር እንዲጋቡ ብትፈቅድ፣ የሌሎች አገሮች ሰዎች”

ስለዚህ የእግዚአብሔር ቁጣ በአንተ ላይ ይነድዳል

ሙሴ የእግዚአብሕርን ቁጣ እሳትን ከሚለኩስ ሰው ጋር ያነጻጽረዋል። ይህ የሚያስቆጣውን ስለሚያጠፋበት ስለ እግዚአብሔር ኃይል አጽንዖት ይሰጣል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በአንተ ላይ እግዚአብሔር ቁጣውን ያነዳል” ወይም “ከዚያም እግዚአብሔር በአንተ ላይ በጣም ይቆጣል” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በአንተ ላይ

“አንተ” የሚለው ቃል እስራኤላውያንን ሁሉ ስለሚመለከት ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

የምታደርጉት -- አፍርሱ -- ስበሩ -- ቁረጡ -- አቃጥሉ

እዚህ ጋ ሙሴ የሚናገረው ለእስራኤላውያን ሁሉ ነው፣ ስለዚህ እነዚህ ቃላት ብቁ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

Deuteronomy 7:6

የተለየ ሕዝብ ናችሁ

እግዚአብሔር ሕዝቡን እስራኤልን የእርሱ እንዲሆኑ በተለየ ሁኔታ መምረጡ ከሌሎች ሕዝቦች እንደለያቸው ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በምድር ፊት ከሚኖሩት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት “በምድር ላይ ከሚኖሩት” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 7:7

ፍቅሩን በእናንተ ላይ አላደረገም

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ሌሎችን ከወደደበት በላይ እናንተን አልወደዳችሁም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በጽኑ እጅ

እዚህ ጋ “ጽኑ እጅ” የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ኃይል ነው። እነዚህ ቃላት በዘዳግም 4፡34 ላይ ደግሞ ይታያሉ። አ.ት፡ “በጽኑ ኃይሉ”(ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 7:9

ለሺህ ትውልድ

“ለ1,000 ትውልድ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ለሚጠሉት በፊታቸው ይበቀላቸዋል

የዚህ የአነጋገር ዘይቤ ትርጉም “እግዚአብሔር እንደቀጣቸው ያውቁ ዘንድ በግልጽና በፍጥነት ይበቀላቸዋል” የሚል ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በሚጠሉት በማናቸውም ላይ አይዘገይም

“አይዘገይም” የሚለው ቃል እግዚአብሔር በብርቱ ይቀጣል የሚለውን አጽንዖት ዝቅ አድርጎ የሚያሳይ ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የሚጠሉትን ሁሉ በብርቱ ይቀጣቸዋል” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 7:12

ያበዛሃል

“የሕዝብህ ቁጥር እንዲበዛ ያደርጋል”

የማህፀንህን ፍሬ

ይህ “ልጆችህን” የሚል የአነጋገር ዘይቤ ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የመሬትህን ፍሬ

ይህ “ምርትህን” የሚል የአነጋገር ዘይቤ ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የከብትህን ብዛት

“ከብትህ እንዲበዛ”

Deuteronomy 7:14

ከሌሎች ሕዝቦች የበለጠ ትባረካለህ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሌሎች ሕዝቦችን ከምባርክበት በበለጠ እባርክሃለሁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በመካከልህ ወይም በከብቶችህ መካከል የማይወልድ ወንድ ወይም መካን ሴት አይኖርም

ሙሴ ሁሉም ልጆች ሊኖሯቸው እንደሚችሉ አጽንዖት ለመስጠት አሉታዊ መግለጫዎችን ይጠቀማል። ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እናንተ ሁላችሁም ልጆች ይኖሯችኋል፣ ከብቶቻችሁም ይበዛሉ” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

በመካከልህ -- ከብቶችህ

“አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት ቃላት ብዙ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

በሽታን ሁሉ ከአንተ አርቃለሁ

“እንደማትታመም እርግጠኛ ሁን” ወይም “ፍጹም ጤና እንድትሆን እጠብቅሃለሁ”

በአንተ ላይ -- ክፉ በሽታዎችን ሁሉ፣ ነገር ግን በሚጠሉህ ሁሉ ላይ ያመጣቸዋል

ሙሴ በሽታን እግዚአብሔር በሰዎች ጫንቃ ላይ እንደሚጭነው ከባድ ቁስ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “እርሱ በየትኛውም ክፉ በሽታ እንድትታመም አያደርግህም … ነገር ግን ጠላቶችህ በእነርሱ እንዲታመሙ ያደርጋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 7:16

ሕዝቦችን ሁሉ ታጠፋቸዋለህ

“ሁሉንም የሕዝብ ወገኖች ፈጽመህ እንድታጠፋቸው አዝሃለሁ”

ዕይንህ አይራራላቸው

ይህ ትዕዛዝ ነው። ሙሴ ዐይን የሚያየው ራሱን ዐይንን እንደሆነ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “የምታየው እንድትራራላቸው እንዲያደርግህ አትፍቀድ” ወይም “የምታደርገው እንደሚጎዳቸው በማየትህ ምክንያት አትራራላቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አታምልክ

“በፍጹም አታምልክ”

ያ ለአንተ ወጥመድ ይሆንብሃል

ሕዝቡ ሌሎች አማልክትን ካመለኩ በወጥመድ እንደሚያዝ እንስሳ ይሆናሉ፣ ከዚያም ማምለጥ አይችሉም። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 7:17

በልብህ ---- ብትል -- አትፍራ

ሀገራቱ ከእነርሱ ይልቅ ብርቱዎች እንደሆኑ ቢያስተውሉም እንኳን ሕዝቡ መፍራት የለባቸውም። አ.ት፡ “ምንም እንኳን በልብህ -- ብትናገር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በልብህ ብትናገር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ብታስብ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እንዴት ላስወጣቸው እችላለሁ?

ሕዝቡ ሌሎች አገራትን ስለ ፈሩበት ስሜት አጽንዖት ለመስጠት ሙሴ በጥያቄ መልክ ይጠቀማል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል።አ.ት፡ “ላሸንፋቸው አልችልም” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አስታውስ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ማስታወስ አለብህ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ዐይኖችህ ዐይተዋል

እዚህ ጋ “ዕይኖችህ” የሚወክለው የሰውን ሁለንተና ነው። አ.ት፡ “ያየኸው” (See: Synecdoche)

ጽኑውን እጅ፣ የተዘረጋችውንም ክንድ

እዚህ ጋ “ጽኑ እጅ” እና “የተዘረጋች ክንድ” የእግዚአብሔርን ኃይል የሚገልጹ ዘይቤአዊ አነጋገሮች ናቸው። ይህንን በዘዳግም 4፡34 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እና በጽኑ ኃይሉ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 7:20

ከዚህም በላይ፣ እግዚአብሔር

“በተጨማሪም፣ እግዚአብሔር”

ተርብ ይልክባቸዋል

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) ሰዎችን እንዲነድፉና እንዲያሳምሙ እግዚአብሔር ትክክለኛ በራሪ ነፍሳትን ይልክባቸዋል፣ ወይም 2) እግዚአብሔር ሕዝቡ እንዲፈሩና እንዲሸሹ ያደርጋቸዋል።

ከአጠገብህ ይጠፋሉ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ከዚህ በኋላ እንዳታያቸው ይሞታሉ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

አታያቸውም

“ከቶ”

ታላቅና የሚያስፈራ አምላክ

“ታላቅና ድንቅ አምላክ” ወይም “ሰዎቹን እንዲፈሩ የሚያደርግ ታላቅ አምላክ”

ጥቂት በጥቂት

“በዝግታ”

Deuteronomy 7:23

በእነርሱ ላይ ድልን ይሰጥሃል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንድታሸንፍ ያስችልሃል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በእነርሱ ላይ ድልን

“ከሌሎች ሕዝቦች በሆኑት ሰራዊቶች ላይ ድልን”

በከፍተኛ ሁኔታ ያደናግራቸዋል

“በአግባቡ ማሰብ እንዳይችሉ ያደርጋቸዋል”

እስኪጠፉ ድረስ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እስክታጠፋቸው ድረስ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከሰማይ በታች ስማቸው እንዲደመሰስ ታደርጋለህ

እስራኤላውያን የእነዚያን አገራት ሕዝቦች በሙሉ ፈጽመው ስለሚያጠፏቸው ወደፊት ማንም አያስታውሳቸውም። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በፊትህ የሚቆም

“አንተን በመቃወም የሚቆም” ወይም “አንተን በመቃወም ራሳቸውን መከላከል”

Deuteronomy 7:25

ታቃጥላለህ

ይህ ትዕዛዝ ነው።

አማልክቶቻቸውን

“የሌሎች ሕዝቦችን አማልክት”

አትቅና -- በእርሱ አትጠመድ

እነዚህ ቃላት አማልክቶቹን እንዲያቃጥሉ በተሰጣቸው መመሪያ ላይ ተጨማሪዎች ናቸው

በእርሱ ትጠመዳለህ

በጣዖታቱ ላይ ያለውን ወርቅ ወይም ብር መውሰድ እንኳን ሕዝቡ እንዲያመልኳቸው ሊያደርጋቸው ይችላል። ይህንን በማድረጋቸው በወጥመድ እንደተያዘ እንስሳ ይሆናሉ። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ወጥመድ ይሆንባችኋል” (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት))

ይህ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር አስጸያፊ ነው

እነዚህ ቃላት ሕዝቡ ጣዖታቱን እንዲያቃጥሉ እግዚአብሔር ለምን እንደፈለገ ይነግሩናል። “አምላካችሁ እግዚአብሔር በጣም ስለሚጠላው ይህንን አድርጉ”

ፈጽመህ ትጠላዋለህ፣ ትጸየፈዋለህም

“መጥላት” እና “መጸየፍ” የሚሉት ቃላት መሠረታዊ ትርጉማቸው አንድ ሆኖ ሳለ ለጥላቻው ጥልቅነት አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “ፈጽመህ ትጠላዋለህ” (See: Doublet)

እርሱ ለጥፋት የተለየ ነው

እግዚአብሔር አንድን ነገር መርገሙና ሊያጠፋው መማሉ ነገሩን ከየትኛውም ነገር ለይቶ እንደሚያስቀምጠው ሆኖ ተነግሯል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እርሱን እግዚአብሔር ለጥፋት ለይቶ አስቀምጦታል” (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊድምፅ የሚለውን ተመልከት))


Chapter 8

1 በሕይወት እንድትኖሩና እንድትበዙ፥ እግዚአብሔርም ለአባቶቻችሁ ወደ ማለላቸው ምድር ገብታችሁ እንድትወርሱአት ዛሬ ለእናንተ የማዝዘውን ትእዛዘትን ሁሉ ጠብቁ። 2 እግዚአብሔር አምላካችሁ በልባችሁ ያለውን፥ ትእዛዘቱን መጠበቃችሁን ወይም አለመጠበቃችሁን ያውቅ ዘንድ ሊፈትናችሁና ትሁት እንድትሆኑ በእነዚህ በአርባ ዓመታት በምድረ በዳ የመራችሁን መንገድ ሁሉ አስቡ። 3 አስጨነቃችሁ፥ እንድትራቡም አደረጋችሁ፥ እንዲሁም እናንተና ልጆቻችሁ፥ አባቶቻችምሁ የማያውቁአቸውን መና መገባችሁ። ይህም ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣው ነገር ሁሉ በሕይወት ይኖራል እንጂ በእንጀራ ብቻ እንደማይኖር ያስታውቃችሁ ዘንድ ነው። 4 በእነዚህ አርባ ዓመታት ውስጥ የለበሳችሁት ልብስ አላረጀም፥ እግራችሁም አላበጠም። 5 ሰውም ልጁን እንደሚገሥጽ እንዲሁም እግዚአብሔር አምላካችሁ እናንተን እንደሚገሥጽ በልባችሁ አስቡ። 6 በመንገዱም እንድትሄዱ እርሱንም እንድትፈሩ የእግዚአብሔ የአምላካችሁን ትእዛዝ ጠብቁ። 7 እግዚአብሔር አምላካችሁ ወደ መልካምና፥ ከሸለቆና ከኮረብታ የውኃ ጅረቶችና ፈሳሾች የሚመነጩ ምንጮች ወዳሉባት ምድር፤ ስንዴና ገብስ፤ 8 በለስና ሮማን፥ ወይራና ማር ወደ ሞሉባት፥ 9 ሳይጎድላችሁ እንጀራ ወደምትበሉባት ምድር፥ አንዳችም ወደማታጡባት፥ ድንጋይዋ ብረት ወደ ሆነ፥ ከተራራዋም መዳብ ወደሚማስባት ምድር አመጣችሁ። 10 እናንተም ትበላላችሁ፥ ትጠግባላችሁ፥ ስለ ሰጣችሁም ስለ መልካሚቱ ምድር እግዚአብሔር አምላካችሁን ትባርካላችሁ። 11 ዛሬ እኔ እናንተን የማዝዛውን ትእዛዘትን፥ ድንጋጌዎችንና ሥርዓቶችን ባለመጠበቅ እግዚአብሔር አምላካችሁን እንዳትረሱ ተጠንቀቁ። 12 ከበላችሁና ከጠገባችሁ ሙሉም ከሆናችሁ በኋላ መልካምም ቤት ሠርታችሁ በዚያ መኖር ከጀመራችሁ በኋላ እንዳትረሱ ተጠንቀቁ። 13 የላምና የበግ መንጋ ከበዛላችሁ በኋላ፥ ብራችሁና ወርቃችሁም፥ ያላችሁም ሁሉ ከበዛላችሁ በኋላ፥ 14 ልባችሁ እንዳይኮራ ከግብፅም ምድር ከባርነት ቤት ያወጣችሁን እግዚአብሔርን እንዳትረሱ ተጠንቀቁ። 15 መርዛማ እባብና ጊንጥ፥ውኃ በሌለባትና ጥማትም ባለባት በታላቂቱና በምታስፈራው ምድረ በዳ የመራችሁን፥ ከዐለት ድንጋይም ውኃን ያወጣላችሁን፥ 16 በመጨረሻም ዘመን መልካም ያደርግላችሁ ዘንድ ሊፈትናችሁ ሊያዋርዳችሁም አባቶቻችሁ ያላውቁትን መና በምድረ በዳ ያበላችሁን እግዚአብሔር አምላካችሁን እንዳትረሱ፥ 17 በልባችሁም፦ ጉልባታችን የእጃችን ብርታት ይህን ሀብት አመጣልን እንዳትሉ። 18 ነገር ግን ዛሬ እንደ ሆነ ለአባቶቻችሁ የማለላችሁን ቃል ኪዳን ያጸና ዘንድ ሀብት ለማከማቸት ጉልበት ሰጥቶአችኋል፥ እግዚአብሔር አምላካችሁን አስቡ። 19 አምላካችሁንም እግዚአብሔርን ብትረሳ ሌሎችንም አማልክት ብትከተል፥ ብታመልካቸውም፥ ብትሰግድላቸውም ፈጽሞ እንደምትጥፉ እኔ ዛሬውኑ እመሰክርባችኋልለሁ። 20 የእግዚአብሔር የአምላካችሁን ቃል ስላልሰማችሁ እግዚአብሔር ከፍታችሁ እንደሚያጠፋቸው እንደ አሕዛብ እንዲሁ እናንተ ትጠፋላችሁ።



Deuteronomy 8:1

በሕይወት እንድትኖሩና እንድትበዙ፣ አባቶቻችሁ -- ገብታችሁ እንድትወርሱ -- መጠበቅ አለብህ

“አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት አገባቦች በሙሉ እንዲሁም ግሦቹ ብዙ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

አስታውስ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ማስታወስ አለብህ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

አርባ ዓመታት

“40 ዓመታት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ትሁት ሊያደርግህ

“ምን ያህል ደካማና ኃጢአተኛ እንደሆንክ ሊያሳይህ”

ለማወቅ

“ለመግለጥ” ወይም “ለማሳየት”

በልብህ የነበረውን

ልብ የሰው ባህርይ ምሳሌ ነው። አ.ት፡ “ምን ዓይነት ሕዝብ እንደሆንክ” ወይም “ባህሪህን እንዴት መግለጥ እንዳለብህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 8:3

ትሁት አደረገህ

“እግዚአብሔር ምን ያህል ደካማና ኃጢአተኛ መሆንህን አሳየህ”። በዘዳግም 8፡2 ላይ “ትሁት ሊያደርግህ” የሚለው ቃል እንዴት እንደተተረጎመ ተመልከት።

መናን መገበህ

“እንድትበላው መናን ሰጠህ”

ሰዎች በሕይወት የሚኖሩት በእንጀራ ብቻ አይደለም

እዚህ ጋ “እንጀራ” የሚወክለው ሁሉንም የምግብ ዓይነት ነው። አ.ት፡ “ሰዎች በሕይወት ለመኖር እንዲችሉ የሚፈልጉት ምግብ ብቻ አይደለም” (See: Synecdoche)

ሰዎች በሕይወት የሚኖሩት ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ነገር ሁሉ ነው

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር አፍ” በፈሊጣዊ አነጋገር እግዚአብሔር የሚናገረው ቃል ማለት ነው። አ.ት፡ “ሰዎች በሕይወት መኖር እንዲችሉ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ መታዘዝ አለባቸው” ወይም “ሰዎች በሕይወት መኖር እንዲችሉ እግዚአብሔር የሚነግራቸውን መፈጸም አለባቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 8:4

አርባ ዓመታት == ልብሳችሁ

ይህ “ማስታወስ” የሚገባቸው የመጨረሻው ንብረታቸው ነው (ዘዳግም 8፡2)

አርባ ዓመታት

“40 ዓመታት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አስቡ == ጠብቁ == በመንገዱ ሂዱ፣ እርሱንም አክብሩት

ይህ በዘዳግም 8፡1-2 የሚጀምረውን የትዕዛዛቱን ዝርዝር የሚቀጥል ነው።

ስለዚህ ነገር በልብህ አስብ

እዚህ ጋ ፈሊጣዊ አነጋገር የሆነው “ልብ” የሚወክለው የአንድን ሰው አሳብና ማስተዋል ነው። አ.ት፡ “አስተውል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 8:7

የ == ምድር

“ከ -- ምድር” ወይም “ -- ያላትን ምድር”

Deuteronomy 8:9

የምትበላውን እንጀራ የማታጣባት ምድር

ይህ ምጸታዊ አነጋገር በአዎንታዊነት ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “የተትረፈረፈ ምግብ የምታገኝበትን ምድር” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

ምንም ነገር የማታጣበትን ሀገር

ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የምትፈልገውን ሁሉ የምታገኝበት” (ድርብ አሉታዊ የሚለውን ተመልከት)

ድንጋዮቹ ብረት የሆኑበት

ድንጋዮቹ በብረት ማዕድን የተሞሉ ናቸው። የብረት ማዕድን ሰይፍና ማረሻ ለመሥራት የሚያገለግል ጠንካራ ብረት ነው።

መዳብ ትቆፍራለህ

“የመዳብ ማዕድን ታወጣለህ”። መዳብ የቤት ውስጥ መገልገያዎችን ለመሥራት የሚያገለግል ለስለስ ያለ ብረት ነው።

ትበላለህ፣ ትጠግባለህም

“እስክትጠግብ ድረስ የምትበላው በቂ ምግብ ይኖርሃል”

ትባርካለህ

“ታመሰግናለህ” ወይም “ምስጋናን ታቀርባለህ”

Deuteronomy 8:11

ትዕዛዞቹን ቸል አትበል

“ትዕዛዞቹን መጠበቅህን አታቁም” ወይም “ትዕዛዛቱን መጠበቅህን ቀጥል”

በበላህና በጠገብህ ጊዜ

“የምትበላው በቂ ምግብ በሚኖርህ ጊዜ”

ልብህ ይነሣሣል

እዚህ ጋ “ልብ” የሚወክለው ውስጠኛውን ሰው ነው። መታበይና ከእንግዲህ እግዚአብሔርን ያለመታዘዝ እንደ ሰው ልብ መነሣሣት ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ትታበያለህ፣ ከእንግዲህም እግዚአብሔርን አትታዘዝም” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 8:13

መንጋዎችህ

“የከብትህ፣ የበግና የፍየል መንጋህ”

መብዛት

በቁጥር እጅግ መጨመር

ያለህ ሁሉ ሲበዛልህ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በጣም ብዙ ነገሮች አሉህ” ወይም “በጣም ብዙ ንብረት አለህ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ልብህ ይነሣሣል

እዚህ ጋ “ልብ” የሚወክለው ውስጠኛውን ሰው ነው። መታበይና ከእንግዲህ እግዚአብሔርን ያለመታዘዝ እንደ ሰው ልብ መነሣሣት ሆኖ ተነግሯል። በዘዳግም 8፡12 ላይ ተመሳሳዩን ሐረግ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ትታበያለህ፣ ከእንግዲህም እግዚአብሔርን አትታዘዝም” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ያወጣህን

ሙሴ ለእስራኤላውያን ስለ እግዚአብሔር የሚያውቁትን ማስታወስ ጀምሯል (ለይቶ ማሳወቅ ማሳወቅን ወይም ማስታወስን ሲቃረን የሚለውን ተመልከት)

ከባርነት ቤት ያወጣህ

ይህ በግብፅ በባርነት የነበሩበትን ጊዜ የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ባሪያዎች ከነበራችሁበት ስፍራ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 8:15

በመጨረሻ -- የመራህን

ሙሴ ለእስራኤላውያን ስለ እግዚአብሔር የሚያውቁትን ማስታወስ ቀጥሏል (ዘዳግም 8፡14)። (ለይቶ ማሳወቅ ማሳወቅን ወይም ማስታወስን ሲቃረን የሚለውን ተመልከት)

የመራህ -- ያመጣህ -- መገበህ

“የመራህ እግዚአብሔር … ያመጣህ እግዚአብሔር … እግዚአብሔር መገበህ”

ተናዳፊ እባብ

“መርዘኛ እባብ”

የተጠማ ምድር

ይህ ሐረግ ልክ ሰው ውሃ በሚፈልግበት ጊዜ እንደሚጠማ ምድሪቱ መጠማቷን ይገልጻል። አ.ት፡ “ደረቅ ምድር” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

መልካም ሊያደርግልህ

“ሊረዳህ” ወይም “ለአንተ መልካም ስለነበረ”

ሆኖም በልብህ -- ትል ይሆናል

ይህ ምናልባት ሰዎች ልባቸው “በሚታበይበት” እና “እግዚአብሔርን በሚረሱበት” ጊዜ የሚያደርጉት ሦስተኛው ነገር ነው። (ዘዳግም 8፡14)። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ኃይሌና የእጄ ብርታት ይህንን ሁሉ ሀብት አስገኘልኝ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚያመለክተው የአንድን ሰው ኃይል ወይም ችሎታ ነው። አ.ት፡ “እኔ በጣም ብርቱና ኃይለኛ ስለሆንኩኝ ይህንን ሀብት አግኝቻለሁ” ወይም “እነዚህን ነገሮች ሁሉ በራሴ ኃይልና ችሎታ አግኝቻለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 8:18

ነገር ግን ትዝ ይበልህ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ትዕዛዝ ነው። አ.ት፡ “ነገር ግን አስታውስ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ያጸና ዘንድ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) “እርሱ በዚህ መንገድ ያጸናል” ወይም 2) “በዚህ መንገድ እርሱ ሊያጸና የታመነ ነው”

ያ -- ዘንድ

“ስለዚህ ይችላል”

ማጽናት

እንዲቆም ወይም እንዲኖር ማድረግ

ዛሬ እንደሆነው ሁሉ

“አሁን እንደሚያደርገው ሁሉ” ወይም “ቃል ኪዳኑን አሁን እንዳጸናው ሁሉ”

ሌሎች አማልክቶችን ብትከተል

መከተል የመታዘዝ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ሌሎች አማልክቶችን ማገልገል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በአንተ ላይ -- ብት -- በፊትህ -- ትጠፋላችሁ -- አትሆኑም -- አምላክህ

“አንተ” የሚሉት እነዚህ አገባቦች ሁሉ ብዙ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

በእናንተ ላይ እመሰክራለሁ

“አስጠነቅቃችኋለሁ” ወይም “በምስክሮች ፊት እነግራችኋለሁ”

በእርግጥ ትጠፋላችሁ

“ያለምንም ጥርጥር ትሞታላችሁ”

በፊታችሁ

“በፊት ለፊታችሁ”

የእግዚአብሔርን ድምፅ ስላልሰማችሁ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” ማለት እግዚአብሔር ያደርጉት ዘንድ ለሕዝቡ የሚነግራቸው ማለት ነው። አ.ት፡ “የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ስላልታዘዛችሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 9

1 እስራኤል ሆይ፥ ስሙ፥ ከእናንተ የበለጡትንና የበረቱትን አሕዛብ፥ እስከ ሰማይም ድረስ የተመሸጉትን ታላላቅ ከተሞች ለመውረስ ትገቡ ዘንድ ዛሬ ዮርዳኖስን ልትሻገሩ ነው፤ 2 የኤናቅ ልጆች ፥ ታላቅና ረጅም ሕዝብ፥ እናንተም የምታውቃቸው ስለ እነርሱም እንዲህ ያላችኋቸው፦ በዔናቅ ልጆች ፊት ማን መቆም ይችላል? 3 ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችሁም እንደሚበላ እሳት ሆኖ በፊታችሁ ስለሚያልፍ፥ ዛሬ እርሱ ያጠፋቸዋል፥ በፊታችሁም ያዋርዳቸዋል፥ እግዚአብሔርም እንደ ተናገራችሁ እናንተ ታሳድዳቸዋላችሁ ፈጥናችሁም ታጠፋቸዋላችሁ። 4 እግዚአብሔር አምላካችሁ ከፊታችሁ ካወጣቸው በኋላ ፦ እንወርሳት ዘንድ ወደዚህች ምድር እግዚአሔር ያመጠን፥ ስለ ጽድቄ ነው፥ እነዚህንም አሕዛብ እግዚአብሔር ከፊታችን ያወጣቸው ኃጢአተኞች ስለ ሆኑ ነው፥ ብላችሁ በልባችሁ እንዳትናገሩ። 5 ምድራቸውን ትወርሱአት ዘንድ የምትገቡት ስለ ጽድቃችሁ ወይም ስለ ልባችሁ ቅንነት አይደለም፤ ነገር ግን እግዚአብሔር አምላካችሁ ከፊታችሁ በሚያጠፋቸው በእነዚያ አሕዛብ ኃጢአት ምክንያትና ለአባቶቻችሁ ለአብርሃም፥ ለይስሐቅና ለያዕቆብ የማለላቸውን ቃል ይፈጽም ዘንድ ነው። 6 እንግዲህ እናንተ አንገተ ደንዳና ሕዝብ ስለ ሆናችሁና እግዚአብሔር አምላካችሁ ይህን መልካም ምድር ርስት አድርጎ የሰጣችሁ ስለጽድቃችሁ እንዳይደለ እወቁ። 7 እግዚአብሔር አምላካችሁን በምድረ በዳ እንዳስቁጣችሁት ከግብፅ አገር ከወጣችሁበት ቀን ጀምሮ ወደዚህ ስፍራ እስከ መጣችሁ ድረስ በእግዚአብሔር ላይ እንዳመፃችሁ አስቡ። 8 በኮሬብ ደግሞ እግዚአብሔርን አስቆጣችሁ፤ እግዚእብሔርም ሊያጠፋችሁ ተቆጣባችሁ። 9 እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር የገባውን የቃል ኪዳን፥ የድንጋዩን ጽላቶችን ከእግዚአብሔር ለመቀበል ወደ ተራራ ወጥቼ በተራራው ላይ ለአርባ ቀናትና አርባ ሌሊት በቆየሁበት ጊዜ እንጀራም አልበለሁም፥ ውኃም አልጠጠሁም። 10 እግዚአብሔርም በእርሱ ጣት የተጻፉትን ሁለቱን የድንጋይ ጽላቶችን ሰጠኝ፤ በጽላቶቹም ላይ በተራራው ሥር በነበረው ጉበዔ እግዚአብሔር በእሳት መካከል ሆኖ የተናገራችሁ ቃል ሁሉ ተጽፎባቸው ነበር። 11 ከአርባ ቀንና ከእርባ ሌሊትም በኋላ እግዚአብሔር ሁለቱን የድግንጋይ ጽላቶች፥ ያቃል ኪዳኑን ጽላቶች ሰጠኝ። 12 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ ተነሥተህ ከዚህ ፈጥነህ ውረድ ከግብፅ ያወጣሃቸው ሕዝብህ ረክሰዋል። ፈጥነው ካዘዝኋቸውም መንገድ ፈቀቅ ብለዋል። ቀልጦ የተሠራ ምስልም ለራሰቸው አድርገዋል። 13 ከዚህም በተጨማሪ እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ተናገረ፦ ይህ ሕዝብ አንገተ ደንዳና መሆኑን አይቼአለሁ። 14 ስለዚህ አጠፋቸው፥ ስማቸውንም ከሰማይ በታች እደመስሳለሁ፥ አንተንም ከእነርሱ ለሚበረታና ለሚበዛ ሕዝብ አደርግሃለሁ። 15 እኔም ተመልሼ ከተራራው ወረድሁ፥ ተራራውም በእሳት ይነድድ ነበር። ሁለቱም የቃል ኪንን ጽላቶች በእጆቼ ነበሩ። 16 እናንተም እግዚአብሔር አምላካችሁን እንደበደላችሁ አየሁ። ለእናንተም ለራሳችሁ የጥጃ ምስል ሠርታችሁ ነበር። እግዚአብሔርም ካዘዛችሁ መንገድ ፈቀቅ ብላችሁ ነበር። 17 ሁሉቱንም ጽላቶች ወስጄ፥ ከእጆቼ ጣልኋቸው። በዓይናችሁም ፊት ሰበርኋቸው። 18 ስለ ሠራችሁት ኃጢአት ሁሉ፥ እርሱንም ለማስቆጣት በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን ነገር ከማድረጋችሁ የተነሣ እንደገና በእግዚአብሔር ፊት አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ወደቅሁ፥ እንጀራም አልበላሁም፥ ውኃም አጠጣሁም ነበር። 19 ምክንያቱም እግዚአብሔር ሊያጠፋችሁ ከተቆጣባችሁ ከቁጣውና ከመዓቱ የተነሣ ስለ ፈራሁ ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር በዚያን ጊዜም ሰማኝ። 20 እግዚአብሔርም አሮንን ሊያጠፋው እጅግ ተቆጣው፤ ስለ አሮንም ደግሞ በተመሳሳይ ሁኔታ ጸለይሁ። 21 ያደረጋችሁትንም ኃጢአት ጥጃውን ወስድሁ በእሳትም አቃጠልሁት፥ አደቅዝቅሁትም፤ ዱቄትም እስኪሆን ድረስ ፈጨሁት። ዱቄቱንም ከተራራ በሚወርድ ወንዝ ጣልሁት። 22 እግዚአብሔርንም በቀቤራ፥ በማሳህ፥ በምኞት መቃብርም አስቆጥታችሁት ነበር። 23 እግዚአብሔርም ውጡ የሰጠኋችሁንም ምድር ውረሱ ብሎ ከቃዴስ በርኔ በላካችሁ ጊዜ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ትእዛዝ ላይ አመፃችሁ፥ በእርሱም አላመናችሁም፤ወይም ድምፁንም አልሰማችሁም። 24 እናንተን ካወቅሁበት ቀን ጀምሮ በእግዚአብሔር ላይ ዓመፀኞች ነበራችሁ። 25 እግዚአብሔር ያጠፋችሁ ዘንድ ስለ ተናገረ በእነዚያ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በእግዚአብሔር ፊት ወደቅሁ። 26 ጌታ በእግዚአብሔርም ፊት እንዲህ ብዬ ጸለይሁ፦ እግዚአብሔር ሆይ፥ በታላቅነትህና በኃያልነትህ ከግብፅ ያወጣቸውን፥ የተበዠሃቸውን ሕዝብህንና ርስትህን አታጥፋ ። 27 አገልጋዮችህን አብርሃምንና ይስሐቅን ያዕቆብንም አስብ፤ የዚህን ሕዝብ ደንዳናነት፥ ክፋቱንና ኃጢአቱን አትመልከት፤ 28 እኛንም ያወጣህባት ምድር ሰዎች እግዚአብሔር ተስፋ ወደ ሰጣቸው ምድር ያገባቸው ዘንድ ስላልቻለ፤ ስለጠላቸውም በምድረ በዳ ሊገድላቸው አወጣቸው ይላሉ። 29 እነርሱም በታላቅ ኃይልህ በጸነችውም ክንድህ ያወጣሃቸው ሕዛብህና ርስትህ ናቸው።



Deuteronomy 9:1

እስራኤል ሆይ፣ ስማ

“እስራኤል” የሚለው ቃል የእስራኤልን ሕዝብ የሚመለከት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ሕዝብ ሆይ፣ ስማ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለመውረስ

“መሬታቸውን ለመውሰድ”

እስከ ሰማይ ድረስ የተመሸጉትን

ይህ ከተሞቹ በጣም ሰፊና ጠንካራ በመሆናቸው ምክንያት ሕዝቡ መፍራታቸውን አጽንዖት ለመስጠት የተደረገ ግነት ነው። በዘዳግም 1፡28 ላይ ተመሳሳዩን ቃላት እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ሰማይ የሚደርሱ የሚመስሉ ግንቦች ነበሯቸው” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

የዔናቅ ልጆች

በጣም ረጃጅምና ኃያላን የነበሩ የዔናቅ ሕዝብ ተወላጆች ናቸው። ተመሳሳዮቹን ቃላት በዘዳግም 1፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።(See: Assumed Knowledge and Implicit Information እና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በዔናቅ ልጆች ፊት ማን መቆም ይችላል?

ይህ ማለት የዔናቅ ልጆች ኃያላን በመሆናቸው ሰዎች ይፈሯቸው ነበር። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በዔናቅ ልጆች ፊት ራሱን መከላከል የሚችል አልነበረም” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 9:3

ዛሬ

ሙሴ ፀሐይ ከጠለቀችበት ጊዜ ጀምሮ ሳይሆን ቀናትና ሳምንታት ስለጀመሩባት ስለዚያች ቀን ማለቱ ነው።

እንደሚባላ እሳት

እግዚአብሔር የሌሎች ሕዝቦችን ሰራዊት ለማጥፋት የሚችል ኃያል ነው። (See: Simile)

በፊትህ ድል ያደርጋቸዋል

“ልትቆጣጠራቸው እንድትችል ደካማ ያደርጋቸዋል”

Deuteronomy 9:4

በልብህ -- አትበል

እዚህ ጋ “በልብህ” ማለቱ “በአሳብህ” ለማለት ነው። አ.ት፡ “በራስህ አታስብ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወግቶ ያስወጣቸዋል

“ሌሎች ሕዝቦችን አሳዶ ሲያስወጣቸው”

Deuteronomy 9:5

በልብህ ቅንነት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። “ዘወትር የምታስበውና የምትመኘው ትክክለኛውን ነገር ስለሆነ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ቃሉ ይፈጸም ዘንድ

“ቃሉ” የሚለው ፈሊጣዊ በሆነ አነጋገር የሚያመለክተው እግዚአብሔር የሰጠውን ተስፋ ነው። አ.ት፡ “ተስፋውን ይፈጽም ዘንድ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለአባቶቻችሁ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ

አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብ ሙሴ ለሚናገራቸው ሰዎች “አባቶቻቸው” ናቸው።

Deuteronomy 9:7

አስታውስ፣ ከቶም አትርሳ

ሙሴ በማስታወስ አስፈላጊነት ላይ አጽንዖት ለመስጠት ተመሳሳዩን ትዕዛዝ በአዎንታዊና በአሉታዊ ቃላት ይደግማቸዋል። አ.ት፡ “ለማስታወስ ተጠንቀቅ” (See: Doublet)

እግዚአብሔርን እንዴት ለቁጣ እንዳነሣሣኸው

እዚህ ጋ “አንተ” የሚያመለክተው ከሙሴ ጋር ያሉትንና በተጨማሪም በቀደመው ትውልድ የነበሩትን እስራኤላውያንን ነው። (See: Forms of You)

ወደዚህ ስፍራ ከመጣህ፣ አመፀኛ ነበርክ -- ለቁጣ አነሣሣኸው -- ሊያጠፋህ

“አንተ” የሚሉት ሁሉም አገባቦች ብዙ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

ወደዚህ ስፍራ

ይህ የሚያመለክተው የዮርዳኖስ ወንዝ ሸለቆን ነው።

Deuteronomy 9:9

የድንጋይ ጽላቶች፣ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ያደረገው የኪዳኑን ጽላቶች

እዚህ ጋ “የድንጋይ ጽላቶች” ይኸውም እግዚአብሔር አሥሩን ትዕዛዛት የጻፈባቸውን መሆኑን ሁለተኛው ሐረግ ግልጽ ያደርጋል። (See: Parallelism)

አርባ ቀንና አርባ ሌሊት

“40 days and 40 nights” “40 ቀንና 40 ሌሊት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር የነገራችሁ ቃል ሁሉ በእነርሱ ላይ ተጽፈው ነበር

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ለእናንተ የነገራችሁን እነዚያኑ ቃላት በእነርሱ ላይ ጻፋቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከእሳት መካከል -- እግዚአብሔር ተናገራችሁ

እግዚአብሔር እንደ ሰው በእሳት መካከል ቆሞ በታላቅ ድምፅ የተናገረ ይመስል ነበር።

በጉባዔ ቀን

የነገር ስም የሆነው “ጉባዔ” እንደ ግሥ “በአንድነት መሰብሰብ” ተብሎ ሊገለጽ ይችላል። አ.ት፡ “እናንተ እስራኤላውያን ሁላችሁ መጥታችሁ በአንድ ስፍራ በተገናኛችሁበት ቀን” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 9:11

አርባ ቀና አርባ ሌሊት

“40 ቀንና 40 ሌሊት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሁለቱን የድንጋይ ጽላቶች፣ የኪዳኑን ጽላቶች

እዚህ ጋ “ሁለቱን የድንጋይ ጽላቶች” የተባሉት እግዚአብሔር አሥሩን ትዕዛዛት የጻፈባቸውን መሆኑን ሁለተኛው ሐረግ ግልጽ ያደርጋል። (See: Parallelism)

ሕዝብህ -- ራሳቸውን አርክሰዋል

“ሕዝብህ … የተሳሳተ ነገር እያደረጉ ነው” እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ካዘዝኳቸው መንገድ ዘወር ብለዋል

ሙሴ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት መጠበቅን በመንገድ ላይ ከመሄድ ጋር አመሳስሎ ይናገራል። አ.ት፡ “ትዕዛዞቼን እምቢ ማለት ጀምረዋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 9:13

ስማቸውን ከሰማይ በታች እንድደመስሰው

“ስማቸው ፈጽሞ እንዲጠፋ አደርጋለሁ” ወይም “ማንም እንዳያስታውሳቸው ሁሉንም እገድላቸዋለሁ”። ተመሳሳዩን ሐረግ በዘዳግም 7፡24 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

Deuteronomy 9:15

ተመለክትሁ

እዚህ ጋ “ተመለከትሁ” የሚለው ቃል ሙሴ ባየው ነገር መደነቁን ያሳያል።

ቀልጦ የተሠራ ጥጃን ለራሳችሁ አበጃችሁ

የእስራኤል የቀደመው ትውልድ ያመልኩት ዘንድ የብረት ጥጃ እንዲሠራላቸው አሮንን ጠየቁት። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

እግዚአብሔር ካዘዛችሁ መንገድ ፈጥናችሁ ወጣችሁ

ሙሴ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት መጠበቅ በመንገድ ላይ ከመሄድ ጋር አመሳስሎ ይናገራል። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 9፡12 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

Deuteronomy 9:17

በዐይኖቻችሁ ፊት ሰባበርኳቸው

እዚህ ጋ “ዐይኖቻችሁ” የእስራኤልን ሕዝብ የሚወክል ምሳሌ ነው። አ.ት፡ “እዚያው በፊት ለፊታችሁ ሰባበርኳቸው” ወይም “ልታዩአቸው በምትችሉበት ስፍራ ሰባበርኳቸው” (See: Synecdoche)

በግምባሬ ተደፋሁ

“በመሬት ላይ በግምባሬ ወደቅሁ”። ይህ እግዚአብሔር ታላቅ እንደሆነና ሙሴ ምንም እንዳይደለ ማሳያ መንገድ ነው።

አርባ ቀንና አርባ ሌሊት

“40 ቀንና 40 ሌሊት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 9:19

እግዚአብሔር ሊያጠፋችሁ የተቆጣበትን ቁጣውንና ጽኑ ቅሬታውን ፈርቼ ነበር

“ቁጣና ጽኑ ቅሬታ” የሚሉት ቃላት እግዚአብሔር ስለ ተቆጣና ቅር ስለተሰኘ ሊያደርግ ያለውን የሚያመለክቱ ፈሊጣዊ አነጋገሮች ናቸው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በእናንተ ተቆጥቶ ነበር -- በእናንተ ላይ እጅግ አዝኖ ነበር -- እስኪያጠፋችሁ ድረስ ተቆጥቶ ነበር፣ እኔም ስለሚያደርገው ነገር ፈርቼ ነበር”

Deuteronomy 9:21

ወሰድኩ -- አቃጠልኩት -- አድቅቄ -- መሬት -- በተንሁት

ሙሴ ምናልባት ሌሎች ሰዎች ሥራውን በቀጥታ እንዲሠሩት አዝዟቸው ይሆናል። አ.ት፡ “የሚወስዱ … የሚያቃጥሉ … የሚሰብሩ … የሚፈጩ … የሚበትኑ ሰዎች ነበሩኝ”

ኃጢአታችሁ፣ የሠራችሁት ጥጃ

እዚህ ጋ የሠሩት የወርቅ ጥጃ ራሱ የእነርሱ “ኃጢአት” መሆኑ ተመልክቷል። አ.ት፡ “በኃጥአተኝነት የሠራችሁት ጥጃ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 9:22

ተቤራ -- ማሳህ -- ቂብሮት ሐታአዋ

እነዚህ የእስራኤል ሕዝብ በምድረ በዳ በነበሩበት ጊዜ የሄዱባቸው የተለያዩ ቦታዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ውጡ

እግዚአብሔር ሊሰጣቸው የነገራቸው ምድር በኮረብታዎቹ ላይ ያለ ሲሆን እነርሱ የነበሩት ቆላው ላይ ነው፣ ስለዚህ ያገኙት ዘንድ ወደ ኮረብታዎቹ መውጣት ነበረባቸው።

በትዕዛዙ ላይ አመፃችሁ

“ትዕዛዝ” የሚለው ቃል እግዚአብሔርን ራሱን የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ላይ አመፃችሁ፤ ትዕዛዙንም አልጠበቃችሁም” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ድምፁን መስማት

እዚህ ጋ “ድምፁን” ማለት እግዚአብሔር ተናግሮችት የነበረውን ነው። አ.ት፡ “የተናገረውን ታዘዙት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ካወቅዃችሁ ጊዜ ጀምሮ

“ልመራችሁ ከጀመርኩበት ጊዜ አንሥቶ”። አንዳንድ ትርጉሞች “ካወቃችሁ ጊዜ ጀምሮ”፣ ለመጀመሪያ ጊዜ እግዚአብሔር እነርሱን ያወቀበት ቀን በሚል ይነበባሉ

Deuteronomy 9:25

በእግዚአብሔር ፊት በግምባር መደፋት

“በመሬት ላይ በግምባሬ ተደፋሁ”። ይህንን በዘዳግም 9፡18 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

አርባ ቀንና አርባ ሌሊት

“40 ቀንና 40 ሌሊት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የተቤዠኸውን

እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ገንዘብ በመክፈል ከባርነት ነጻ እንዳደረጋቸው በሚመስል መልኩ ሙሴ ይናገራል። አ.ት፡ “አድነሃቸዋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በታላቅነትህ

“ታላቅነት” የሚለው ቃል የእግዚአብሔርን ታላቅ ኃይል የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “በታላቅ ኃይልህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በብርቱ እጅ

እዚህ ጋ “ብርቱ እጅ” የሚያመለክተው የእግዚአብሔርን ኃይል ነው። ተመሳሳዮቹን ቃላት በዘዳግም 4፡34 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “በብርቱ ኃይልህ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 9:27

አስብ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አስታውስ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እኛን ከዚያ ያመጣህበት ያ ምድር

“ያ ምድር” የሚሉት ቃላት የግብፅን ሕዝብ የሚያመለክቱ ፈሊጣዊ አነጋገሮች ናቸው። “ስለዚህ የግብፅ ሰዎች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ይላሉ

“ሊሉ ይችላሉ”

በታላቅ ኃይልህና በተዘረጋች ጉልበትህ

እነዚህ ሐረጎች መሠረታዊ አሳባቸው አንድ ሆኖ ሕዝቡን ለማዳን እግዚአብሔር በተጠቀመበት ታላቅ ኃይሉ ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Doublet)


Chapter 10

1 በዚያን ጊዜም እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፦ እንደ መጀመሪያ ያሉትን ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ጠርበህ ወደ እኔ ወደ ተራራ ውጣ፤ ለአንተም የእንጨት ታቦት ሥራ። 2 በሰበርሃቸው በመጀመሪያዎቹ ጽላቶች ላይ የነበሩትን ቃላት በእነዚህ ጽላቶች ላይ እጽፋለሁ፤ አንተም በታቦቱ ውስጥ ታደርጋቸዋለህ። 3 ከግራርም እንጨት ታቦትን ሠራሁ፥ እንደፊተኞቹም ሁለት የድንጋይ ጽላቶች ጠረብሁ፥ ሁለቱንም ጽላቶች በእጄ ይዤ ወደ ተራራው ወጣሁ። 4 በተራራው ሥር የጉባዔው ቀን እግዚአብሔር በተራራው ላይ በእሳት መካከል ሆኖ የተናገራችሁን አሥርቱን ቃላት በመጀመሪያ ተጽፈው እንደ ነበረ በጽላቶቹ ላይ ጻፈ፤ ከዚያም እግዚአብሔር እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ። 5 ተመልሼም ከተራራው ወረድሁ፤ ጽላችቶችንም በሠረሁት ታቦት ውስጥ አደረግኋቸው፤እግዚአብሔርም እንዳዘዘኝ በዚያ ሆኑ። 6 የእስራኤልም ልጆች ከብኤሮት ብኔ ያዕቃን ወደ ሞሴራ ተጓዙ። በዚያ አሮን ሞተ፥ በዚያም ተቀበረ፥ በእርሱም ፋንታ ልጁ አልዓዛር ካህን ሆኖ አገለገለ። 7 ከዚያም ወደ ጉድጎዳ ተጓዙ፤ከጉድጎዳም ወደ ውኃ ምንጮች ምድር ወደ ዮጥባታ ተጓዙ። 8 በዚያን ጊዜም እግዚአብሔር የሌዊን ነገድ እግዚአብሔርን ቃል ኪዳን ታቦት ይሸከሙና እርሱንም እንዲያገለግሉ፥ በፊቱም ይቆሙ ዘንድ በስሙም እንዲባርኩ መረጠ። 9 ስለዚህ ለሌዊ ከወንድሞቹ ጋር ክፍልና ርስት የለውም፤ አምላካችሁ እግዚአብሔር እንደ ተናገረው እግዚአብሔር ርስቱ ነው። 10 በተራራውም ላይ እንደ መጀመሪያውም አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ቆየሁ። እግዚአብሔርም እንደገናም ሰማኝ፤ እግዚአብሔርም ሊያጠፋችሁ አልፈለገም። 11 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ ተነሥተህ በሕዝቡ ፊት ሆነህ ሕዝቡን በጉዞው ምራው፤ ለአባቶቻቸው የማለሁላቸውን ምድር ሄደው ይገባሉ። 12 እስራኤል ሆይ፥ አሁንስ አምላክህን እግዚአብሔርን ትፈራ ዘንድ በመንገዱም ሁሉ ትሄድ ዘንድ፥ አምላክህንም እግዚአብሔርን ትውድድ ዘንድ፥ በፍጹም ልብህ፥ በፍጹምም ነፍስህ ታመልከው ዘንድ መልካምም እንዲሆንልህ 13 ዛሬ ለአንተ የማዘዘውን የእግዚአብሔርን ትእዛዝና ሥርዓት ትጠብቅ ዘንድ ከሆነ በቀር እግዚአብሔር አምላክህ ከአንተ የሚፈልገው ምንድን ነው? 14 እነሆ፥ ሰማይና ሰማየ ሰማያትም፥ ምድርም በእርስዋም ያለው ሁሉ የእግዚአብሔር የአምላካችሁ ነው። 15 ብቻ እግዚአብሔር ስለ አባቶቻችሁ ደስ ተሰኝቶአል፥ እነርሱንም ወድዶቸዋል፤ ከእነርሱም በኋላ እናንተን ዘራችሁን እንደ ዛሬው ሁሉ ከአሕዝብ ሁሉ መካከል መረጣችሁ። 16 ስለዚህ እናንተ የልባችሁን ሸለፈት ግረዙ፥ አንገተ ደንዳኖች አትሁኑ። 17 እግዚአብሔር አምላካችሁ የአማልክት አምላክ የጌቶችም ጌታ፥ ታላቅ አምላክ ኃያልም የሚያስፈራም በፍርድ የማያደላ፥ መማለጃም የማይቀበል። 18 እግዚአብሔር ለድሃ አደጉና ባል ለሞተባት ይፈርዳል፥ ምግብና ልብስም የሚሰጥ ነው። 19 ስለዚህ እናንተም በግብፅ አገር ስደተኞች ስለ ነበራችሁ ስደተኛውን ውደዱ። 20 እግዚአብሔር አምላካችሁን ፍሩ፥ እርሱንም አምልኩት። በእርሱም ተጣበቁ፤ በስሙም ማሉ። 21 እርሱ ዓይኖቻችሁ ያዩትን እነዚህን ታላላቆችንና የሚያስፈሩትን ነገሮች ያደረገላችሁ ክብራችሁ ነው፤ አምላካችሁም ነው፤ ። 22 አባቶቻችሁ ሰባ ሰዎች ሆነው ወደ ግብፅ ሄዱ፤ አሁንም እግዚአብሔር አምላካችሁ ብዛታችሁን እንደ ሰማይ ክዋክብት አደረገ።



Deuteronomy 10:1

በዚያን ጊዜ

“ጸሎቴን ከጨረስኩ በኋላ”

የመጀመሪያው

ይህ የሚያመለክተው ሙሴ የሰበራቸውን የመጀመሪያዎቹን ጽላቶች ስብስብ ነው። አ.ት፡ “ቀድሞ በነበሩህ ጽላቶች” (See: Ellipsis እና ደረጃን አመልካች ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በተራራው

ይህ የሲና ተራራን ያመለክታል።

Deuteronomy 10:3

የመጀመሪያው

ይህ የሚያመለክተው ሙሴ የሰበራቸውን የመጀመሪያዎቹን ጽላቶች ስብስብ ነው። አ.ት፡ “ቀድሞ በነበሩኝ ጽላቶች” (Ellipsis እና ደረጃን አመልካች ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ወደ ተራራው ወጣ

“ወደ ሲና ተራራ ወጣ”

ከእሳቱ መካከል

እግዚአብሔር እንደ ሰው በእሳት መካከል ቆሞ በታላቅ ድምፅ የሚናገር ይመስል ነበር። ይህንን በዘዳግም 9፡10 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

በጉባዔው ቀን

የነገር ስም የሆነው “ጉባዔ” “በአንድነት መሰብሰብ” በሚል ግሥ መነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 9፡10 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 10:5

ተመለስኩኝ

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው ሙሴን ነው።

ከተራራው ወረድኩ

x

Deuteronomy 10:6

የእስራኤል ሕዝብ -- የውሃ ምንጮች ወዳሉባት ምድር

ይህ የእስራኤል ሕዝብ ወዴት እንደተጓዙ ዳራዊ መረጃ ይሰጣል። አሮንን በሞሴራ ተፈጥሮአዊ ሞት መሞቱን ደግሞ ያስታውቃል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ከብኤሮት ብኔያዕቃን ወደ ሞሴራ -- ጉድጎዳ -- ዮጥባታ

እነዚህ የእስራኤል ሕዝብ በምድረ በዳ በነበሩበት ጊዜ የሄዱባቸው የተለያዩ ቦታዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ብኤሮት ብኔያዕቃን

ተርጎሚው፣ “’ብኤሮት ብኔያዕቃን’ የሚለው ስም ‘የያዕቃን ሰዎች የውሃ ጉድጓድ’ ማለት ነው” የሚል የግርጌ ማስታወሻ መጨመር ይኖርባቸው ይሆናል።

በዚያ ተቀበረ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እርሱን የቀበሩት በዚያ ነው” ወይም “እስራኤላውያን በዚያ ቀበሩት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

አልዓዛር

ይህ የአሮን ልጅ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 10:8

ያገለግለው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት እንዲቆም

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። “እግዚአብሔር የሚያዘውን መስዋዕት እንዲያቀርብ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በስሙ

እዚህ ጋ “ስም” ሥልጣንን ያመለክታል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር ተወካዮች ሆነው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እንደዛሬው

“ዛሬ እንደሚያደርጉት”

የመሬት ድርሻም ሆነ ርስት

የሌዊ ነገድ ወደዚያ በደረሱ ጊዜ ከተስፋይቱ ምድር ድርሻቸውን አልተቀበሉም። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በይበልጥ ግልጽ መደረግ ይችል ይሆናል።(See: Assumed Knowledge and Implicit Informa- tion)

እግዚአብሔር ርስቱ ነው

እግዚአብሔር ሌዊና ተወላጆቹ ከእርሱ ጋር ስለሚኖራቸው የተለየ ዝምድና ሲናገር ራሱን ሊወርሱት እንደሚችሉ አንዳች ነገር አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “እነርሱ የሚኖራቸው እግዚአብሔር ነው” ወይም “እግዚአብሔር እርሱን እንዲያገለግሉት ይፈቅድላቸዋል፣ በዚያም አገልግሎት የሚያስፈልጋቸውን ያቀርብላቸዋል”

አምላክህ እግዚአብሔር

እዚህ ጋ፣ ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “የአንተ” የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

ነገረው

“ለሌዊ ነገድ ተናገራቸው”

Deuteronomy 10:10

እንደ መጀመሪያው ጊዜ

“አንደኛ” የአንድ መደበኛ ቁጥር ነው። እዚህ ጋ፣ ሙሴ ለመጀመሪያ ጊዜ የድንጋይ ጽላቶችን ከእግዚአብሔር ለመቀበል ወደ ሲና ተራራ የወጣበትን ያመለክታል” (መደበኛ ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

አርባ ቀንና አርባ ሌሊት

“40 ቀንና 40 ሌሊት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሊያጠፋህ

ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

ምድሪቱን እንዲወርሱ

“ምድሪቱን ውሰድ” ወይም “ምድሪቱን ተረከብ”

ለአባቶቻቸው

ይህ የሚያመለክተው አብርሃምን፣ ይስሐቅንና ያዕቆብን ነው።

ልሰጣቸው

“የምሰጥህን፣ ለአባቶቻቸው”

Deuteronomy 10:12

አሁንም እስራኤል

እዚህ ጋ “እስራኤል” የሚለው በፈሊጣዊ አነጋገር የእስራኤልን ሕዝብ ያመለክታል። አ.ት፡ “አሁንም፣ የእስራኤል ሕዝብ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አምላክህ እግዚአብሔር ከአንተ የሚፈልገው ምንድነው? መልካም እንዲሆንልህ ትፈራው ዘንድ እንጂ

ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ ለማስተማር በጥያቄ ይጠቀማል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር እንድታደርገው የሚፈልገው ይህንን ነው፤ መልካም እንዲሆንልህ ትፈራው ዘንድ” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

በመንገዱም ሁሉ ትሄድ ዘንድ

እግዚአብሔርን መታዘዝ በመንገድ ላይ እንደመሄድ መሆኑን ሙሴ ይናገራል። አ.ት፡ “ትዕዛዙን ሁሉ ትጠብቅ ዘንድ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በሙሉ ልብህና በሙሉ ነፍስህ

እዚህ ጋ፣ “ልብ” እና “ነፍስ” የሰውን ውስጣዊ ማንነት የሚመለከት ፈሊጣዊ ንግግር ነው። እነዚህ ሁለት ሐረጎች “በፍጹም” ወይም “በቅንነት” ለማለት በአንድነት ጥቅም ላይ ውለዋል። እነዚህን ሐረጎች በዘዳግም 4፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 10:14

ተመልከት

“ልነግርህ ያለሁት እውነትና ጠቃሚ ስለሆነ ለ -- አስተውል”

ሰማይ -- ምድር

እነዚህ ቃላት ሁለት ጽንፎች ተጣምረው በሁሉም ቦታ ያሉ ሁሉም ነገሮች የእግዚአብሔር መሆናቸውን ያሳያሉ። (See: Merism)

የሰማይ ሰማያት

ይህ በሰማያት ያሉትን ከፍ ያሉ ስፍራዎች ያመለክታሉ። በሰማያት ያሉ ነገሮች በሙሉ የእግዚአብሔር ናቸው።

መርጧችኋል

እዚህ ጋ፣ “አንተ” የሚለው ቃል እስራኤላውያንን በሙሉ የሚመለከት በመሆኑ ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

Deuteronomy 10:16

ስለሆነም

“በዚህ ምክንያት”

የልባችሁን ሸለፈት ግረዙት

“ሸለፈት” የሚለው ቃል በመገረዝ ጊዜ የሚወገደውን የወንድ አካል ሽፋን ያመለክታል። እዚህ ጋ፣ ሙሴ የሚያመለክተው መንፈሳዊ መገረዝን ነው። ይኸውም፣ ሕዝቡ ከሕይወታቸው ኃጢአትን ማስወገድ አለባቸው ማለት ነው። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የአማልክት አምላክ

“ገናናው እግዚአብሔር” ወይም “ብቸኛው እውነተኛ አምላክ”

የጌቶች ጌታ

“ገናናው ጌታ” ወይም “ታላቁ ጌታ”

የሚያስፈራው

“ሰዎች እንዲፈሩ የሚያደርጋቸው”

Deuteronomy 10:18

አባት ለሌላቸው በፍትሕ ይፈርዳል

“ሰዎች አባት የሌላቸውን በፍትሐዊነት እንዲይዙ እግዚአብሔር ያረጋግጣል”

አባት የሌላቸው

እነዚህ ወላጆቻቸው የሞቱባቸውና የሚንከባከባቸው ዘመድ የሌላቸው ልጆች ናቸው።

መበለት

እውነተኛ መበለት ባሏ የሞተባትና በእርጅና ዕድሜዋ የሚረዳት ልጅ የሌላት ሴት ናት።

ስለዚህ

“በዚህ ምክንያት”

Deuteronomy 10:20

እርሱን አምልከው

“ልታመልከው የሚገባህ እርሱን ነው”

ከእርሱ ጋር ተጣበቅ

ከእግዚአብሔር ጋር መልካም ግንኙነት መኖርና በእርሱ ላይ ሙሉ በሙሉ መታመን ከእግዚአብሔር ጋር መጣበቅ በሚል መልኩ ተነግሯል። አ.ት፡ “በእርሱ ላይ መታመን አለብህ” ወይም “ልትታመንበት የሚገባህ በእርሱ ላይ ነው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በስሙም ማል

በእግዚአብሔር ስም መማል ማለት እግዚአብሔርን የተደረገው መሐላ መሠረት ወይም ኃይል ማድረግ ማለት ነው። እዚህ ጋ፣ “ስም” የሚወክለው እግዚአብሔርን ራሱን ነው። በዘዳግም 6፡13 ላይ ተመሳሳዩን ሐረግ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ትምላለህ፣ እግዚአብሔር እንዲያጸናውም ትጠይቀዋለህ” ወይም “በምትምልበት ጊዜ ስሙን ትጠራለህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዐይኖችህ ያዩትን

እዚህ ጋ፣ “ዐይኖች” የሚያመለክተው የሰውን ሁለንተና ነው። አ.ት፡ “አንተ ራስህ ያየኸውን” (See: Synecdoche)

እርሱ ምስጋናህ ነው

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) “ልታመሰግን የሚገባህ እርሱን ነው” ወይም 2) “አንተ ስለምታመሰግነው ሌሎች ሕዝቦች ያመሰግኑሃል”

Deuteronomy 10:22

ወደ ግብፅ ወረዱ

“በስተደቡብ ወደ ግብፅ ወረዱ” ወይም “ወደ ግብፅ ሄዱ”

ሰባ ሰዎች

“70 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

እንደ ሰማይ ከዋክብት አብዝቶሃል

ይህ ከሙሴ ጋር የነበሩት እስራኤላውያን ቁጥራቸው እጅግ ብዙ እንደነበር አጽንዖት ይሰጣል። አ.ት፡ “መቁጠር ከምትችለው በላይ” (See: Simile)


Chapter 11

1 ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችሁን ውዳዱት፥ ሁልጊዜም መመሪያዎቹን፥ ሥርዓቶቹን፥ ድንጋጌዎችንና ትእዛዛትን ጠብቁ። 2 የእግዚአብሔርን የአምላካችሁን ቅጣት፥ታላቅነቱን፥ ኃያልነቱን፥ የተዘረጋውንም ክንዱን፥ ላላወቁት ወይም ላላዩት ልጆቻችሁ እየተናገርሁ እንዳልሆነ አስታውሉ፤ 3 በግብፅም መካከል በንጉሡ በፈርዖንና በአገሩ ሁሉ ላይ ያደረጋውን ተአምራቱንና ሥራውን፥ 4 በተከተሉአችሁም ጊዜ በግብፅ ጭፍራ፥ በፈረሶቻቸውና በሰረገሎቻቸው ያደረገውን፥በኤርትራ ባሕር ውኃ እንዳሰጠማቸው፥ እግዚአብሔርም እስከ ዛሬ ድረስ እንዳጠፋቸው፥ 5 ወደዚህ ስፍራ እስከትመጡ ድረስ በምድረ በዳ ያደረገላችሁን፥አይተዋል። 6 በእስራኤልም ሁሉ መካከል ምድር አፍዋን ከፍታ እነርሱንና ቤተ ሰቦቻቸውን ድንኳኖቻቸውንም ለእነርሱም የነበራቸውን ሁሉ በዋጠቻቸው በሮቤል ልጅ፥ በኤልያብ ልጆች፥ በዳታንና በአቤሮን እግዚአብሔር ያደረገውን አላዩም። 7 ነገር ግን እግዚአብሔር ያደረገውን ታላቁ ሥራ ሁሉ ዓይኖቻቸው አይተዋል። 8 እንግዲህ እንድትጠነክሩ ትወርሱአትም ዘንድ ወደምትሄዱባት ምድር እንድትሄዱ ዛሬ ለእናንተ የማዘዘውን ትእዛዝ ሁሉ ጠብቁ፤ 9 እግዚአብሔርም ለአባቶቻችሁና ለዘራቸው ይሰጣቸው ዘንድ በማለላቸው ወተትና ማርም በምታፈስሰው ምድር ዕድሜአችሁ እንዲረዘም ትእዛዘትን ጠብቁ። 10 ትወሱአት ዘንድ የምትሄዱባት ምድር በመጣችሁበት በግብፅ አገር ዘር እንደዘራችሁና ውኃ በእግራችሁ ታጠጡ እንደነበረ፥ እንደ አትክልት ቦታ አይደለችም፤ 11 ነገር ግን ትወርሱአት ዘንድ ተሻግራችሁ የምትገቡባት ምድር ኮረብታና ሸለቆ ያለባት በሰማይ ዝናብ ውኃ የምትጠጣ አገር ናት፤ 12 አምላካችሁ እግዚአብሔር የሚንከባከባት፤ ከዓመቱ መጀመሪያ እስከ መጨረሻ ድረስ የእግዚአብሔር የአምላካችሁ ዓይን ሁልጊዜ በእርስዋ ላይ የሆነ አገር ናት። 13 እንዲህም ይሆናል፤ እናንተ እግዚአብሔር አምላካችሁን ፥ በፍጹም ልባችሁ፥ በፍጹም ነፍሳችሁ፥ ትወድዱና ታገለግሉት ዘንድ ዛሬ የማዝዛችሁን ትእዛዘትን ፈጽማችሁ ብትሰሙ፥ 14 እህላችሁን፥ ወይናችሁን፥ ዘይታችሁን ትሰበስቡ ዘንድ በየዚዜው ለምድራችሁ የመጀመሪያውንና የኋለኛውን የወቅቱን ዝናብ ይሰጣችኋል። 15 በሜዳ ለእንስሶቻችሁም ሣርን እሰጣለሁ፤ትበላላችሁ፣ ትጠግባላችሁም። 16 ልባችሁ እንዳይስት ፈቀቅ እንዳትሉ ሌሎችንም አማልክት እንዳታመልኩ፥ እንዳትሰግዱላቸውም፥ 17 የእግዚአብሔርም ቁጣ እንዳይነድድባችሁ ዝናብ እንዳይዘንብ ምድሪቱም ፍሬዋን እንዳትሰጥ ሰማይን እንዳይዘጋባችሁ፤ እግዚአብሔርም ከሚሰጣችሁ ከመልካሚቱ ምድር ፈጥናችሁ እንዳትጠፉ ተጠንቀቁ። 18 ስለዚህ እነዚህን ቃሎች በልባችሁና በነፍሳችሁ አኑሩ፤እነርሱንም ለምልክት በእጃችሁ ላይ እሰሩአቸው፥ በዓይኖቻችሁም መካከል እንደ ክታብ ይሁኑላችሁ። ፥ 19 በቤታችሁም ስትቀመጡ፥ በመንገድ ላይም ስትሄዱ፥ ስትተኙ፥ ስትነሡም ልጆቻችሁንም አስተምሩአቸው። 20 በቤታችሁ መቃኖችና በከተሞቻችሁ በሮች ላይ ጻፈው፥ 21 እግዚአብሔርም እንዲሰጣቸው ለአባቶቻችሁ በማለላቸው ምድር፥ እንደ ሰማይ ቀኖች በላይ በምድር ከፍ ያሉና የልጆቻችሁም ዘመን የረዘመ ይሁን ። 22 እግዚአብሔር አምላካችሁን ትወድዱ ዘንድ በመንገዱም ሁሉ ትሄዱ ዘንድ፥ ከእርሱም ጋር ትጣበቁ ዘንድ፥ ዛሬ ለእናንተ የማዝዘውን ትእዛዘት ሁሉ ብትጠብቁ፥ ብታደርጉአቸውም፥ 23 እግዚአብሔር እነዚህን አሕዛብ ሁሉ ከፊታችሁ ያወጣል፤ ከእናንተም የሚበልጡትን፥ የሚበረቱትንም አሕዛብ ትወርሳላችሁ። 24 የእግራችሁ ጫማ የሚረግጥበት ስፍራ ሁሉ ለእናንተ ትሆናለች፤ ከምድረ በዳም ከሊባኖስ ወንዝ፥ ከኤፍራጥስ ወንዝ ጀምሮ እስከ ምዕራብ ባሕር ድረስ ዳርቻችሁ ይሆናል። 25 በእናንተም ፊት ማንም መቆም አይችልም፤ አምላካችሁ እግዚአብሔር እርሱ እንደ ተናገራችሁ ማስፈራታችሁና ማስደንገጣችሁ በምትረግጡበት ምድር ሁሉ ላይ ያኖራል። 26 እነሆ፥ ዛሬ በፊታችሁ በረከትንና መርገምን አኖራለሁ፤ 27 በረከትም የሚሆነው፥ እኔ ዛሬ ለእናንተ የማዝዘውን የእግዚአብሔር የአምላካችሁን ትእዛዝ ብትሰሙ 28 እንዲሁም መርገም የሚሆነው የእግዚአብሔር የአምላካችሁን ትአዛዝ ባትሰሙ፥ ዛሬም ካዘዝኋችሁ መንገድ ፈቀቅ ብትሉ፥ ሌሎችንም የማታውቋቸውን አምልክት ብትከተሉ ነው። 29 እግዚአብሔር አምላካችሁ ትወሱአት ዘንድ እናንተም ወደምትሄዱባት ምድር ባገባሃችሁ ጊዜ፥ በረከቱን በገሪዛን ተራራ፥ መርገሙንም በጌባል ተራራ ይሆናል። 30 እነርሱም በዮርዳኖስ ማዶ ከምዕራብ ካለው መንገድ በኋላ በዓረባ በሚኖሩት በከነዓናውያን ምድር በጌልገላ ፊት ለፊት በሞሬ የአድባር ዛፍ አጠገብ አይደለምን? 31 እግዚአብሔር አምላካችሁ የሚሰጣችሁን ምድር ትወርሱ ዘንድ ዮርዳኖስን ትሻገራላችሁ፥ ትወርሱአታላችሁ፥ ትቀመጡባታላችሁም። 32 እኔም ዛሬ በፊታችሁ የማኖራውን ሥርዓትና ድንጋጌዎች ሁሉ ታደርጉ ዘንድ ጠብቁ።



Deuteronomy 11:1

ሁልጊዜ ጠብቅ

“ሁልጊዜ ታዘዝ”

Deuteronomy 11:2

ያላወቁትም ሆኑ ያላዩት

“ያልተለማመዱት”

ጽኑ እጁን ወይም የተዘረጋች ክንዱን

እዚህ ጋ፣ “ጽኑ እጅ” እና “የተዘረጋች ክንድ” የተባሉት የእግዚአብሔርን ኃይል የሚያመለክቱ ዘይቤአዊ አነጋገሮች ናቸው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡34 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ወይም ጽኑ ኃይሉን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በግብፅ መካከል

“በግብፅ ውስጥ”

በሀገሩ ሁሉ ላይ

እዚህ ጋ፣ “ሀገር” የሚወክለው ሕዝቡን ነው። አ.ት፡ “በሕዝቡ ሁሉ ላይ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 11:4

እርሱ ያደረገውን አላዩም

“እግዚአብሔር ያደረገውን ልጆቻችሁም ቢሆኑ አላዩም”

በግብፅ ሰራዊት

“በግብፅ ወታደሮች”

እናንተን አሳደዷችሁ

እዚህ ጋ “እናንተ” ማለት ከ40 ዓመታት በፊት የነበሩትን እስራኤላውያን ማለት ነው።

ወደዚህ ስፍራ

ይህ ማለት ሙሴ ወደ ከነዓን ከመሻገራቸው በፊት ሲናገራቸው የነበረበት ከዮርዳኖስ ሸለቆ አጠገብ ያለ ሜዳ ነው።

Deuteronomy 11:6

የኤልያብ ልጆች ዳታንና አቤሮን

ሙሴ የሚያመለክተው ዳታንና አቤሮን በሙሴና በአሮን ላይ ያመፁበትን ያለፈውን ጊዜ ሁነት ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በይበልጥ ግልጽ መደረግ ይችላል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ዳታን -- አቤሮን -- ኤልያብ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የሮቤል ልጅ

“የሮቤል ተወላጆች”

መሬት አፏን ከፍታ ዋጠቻቸው

እግዚአብሔር ምድሪቱ ተሰንጥቃ ሰዎች እንዲወድቁበት ማድረጉ ምድር አፍ እንዳላትና ሰዎችን የመዋጥ ችሎታ እንዳላት ተደርጎ ተነግሯል። (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

የተከተላቸው ሕይወት ያለው ሁሉ

ይህ የሚያመለክተው አገልጋዮቻቸውንና እንስሶቻቸውን ነው።

በእስራኤላውያን ሁሉ መካከል

ይህ ማለት በዳታን፣ በአቤሮን፣ በእንስሶቻቸውና በንብረታቸው ላይ ስለሆነው ነገር የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ ምስክሮች ናችው።

ነገር ግን ዐይኖቻችሁ አይተዋል

እዚህ ጋ “ዐይኖች” የሚወክሉት የሰውን ሁለንተና ነው። አ.ት፡ “ነገር ግን እናንተ አይታችኋል” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 11:8

ምድሪቱን መውረስ

“ምድሪቱን መውሰድ

ለመውረስ የምትገቡባት

የእስራኤል ሕዝብ የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግረው ወደ ከነዓን መግባት ስለነበረባቸው “የምትገቡባት” የሚለው ሐረግ ጥቅም ላይ ውሏል።

ረጅም ቀናት

ረጅም ቀናት ረጅም ዕድሜን የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ረጅም ዘመን መኖር እንድትችል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወተትና ማር የምታፈስ ምድር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ይህንን በዘዳግም 6፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “የተትረፈረፈ ወተትና ማር የሚፈስባት ምድር” ወይም “ለከብት ዕርባታና ለእርሻ ምርጥ የሆነ ምድር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 11:10

በእግርህ ውሃ እንዳጠጣሃት

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) “እግር” ወደ እርሻዎቹ ውሃ የመሸከምን ከባድ ሥራ የሚወክል ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ውሃ ለማጠጣት ምድከሙን” ወይም 2) ውሃ የጠጣውን እርሻ በእግሮቻቸው መገልበጥ ነበረባቸው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እጽዋት የሚበቅሉበት ስፍራ

“የአትክልት ስፍራ” ወይም “የልዩ ልዩ አትክልት ስፍራ”

ከሰማያት የዝናብን ውሃ የምትጠጣ

ምድሪቱ ብዙ ዝናብ መቀበሏና መምጠጧ ልክ ምድሪቱ ውሃውን እንደምትጠጣው ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ከሰማይ የሚወርደው ዝናብ የተትረፈረፈ ውሃ ይሰጣታል” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

የአምላክህ የእግዚአብሔር ዐይን ዘወትር በእርሷ ላይ ነው

እዚህ ጋ “ዐይኖች” የሚወክሉት ትኩረትንና ክብካቤን ነው። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር ዘወትር ይመለከታታል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከዓመቱ መጀመሪያ እስከ ዓመቱ መጨረሻ ድረስ

እዚህ ጋ “መጀመሪያ” እና “መጨረሻ” የሚሉት ሁለት ጽንፎች በአንድነት ጥቅም ላይ የዋሉት ዓመቱን በሙሉ ለማለት ነው። አ.ት፡ “ሙሉውን ዓመት ባለማቋረጥ” (See: Merism)

Deuteronomy 11:13

ብታደርጉ ይሆናል

ይህ ማለት እስራኤላውያን እግዚአብሔር ያዘዛቸውን ከታዘዙ እርሱ የሰጣቸውን ተስፋ ይፈጽምላቸዋል።

እኔ የማዝህን

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው ሙሴን ነው።

በሙሉ ልብህና በሙሉ ነፍስህ

“በሙሉ ልብህ” የሚለው የአነጋገር ዘይቤ “በፍጹም” ማለት ሲሆን “በ . . . ነፍስህ” ማለት “በሁለንተናህ” ማለት ነው። እነዚህ ሁለት ሐረጎች ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው። ይህንን በዘዳግም 4፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “በሁለንተናህ” ወይም “በሙሉ ኃይልህ” (የአነጋገር ዘይቤ እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

ለምድርህ ዝናብን በወቅቱ እሰጣለሁ

“በተገቢው ወቅት በምድርህ ላይ ዝናብ እንዲዘንብ አደርጋለሁ”

እሰጣለሁ

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ነው። ይህ በሦስተኛ መደብ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ይሰጣችኋል” ወይም “እርሱ ይሰጣችኋል”

የመጀመሪያውንና የኋለኛውን ዝናብ

ይህ የሚያመለክተው በመጀመሪያ በዘር ወቅት የሚዘንበውን ዝናብና ሰብሉን ለምርትነት የሚያበቃውን ዝናብ ነው። አ.ት፡ “የመከርንና የፀደይን ዝናብ” ወይም “ዝናብን በወቅቱ”

Deuteronomy 11:16

ለራሳችሁ ተጠንቀቁ

“ተጠንቀቁ” ወይም “ልብ በሉ”

ልባችሁ እንዳይታለል

እዚህ ጋ “ልብ” የሚወክለው የአንድን ሰው ምኞት ወይም አሳብ ነው። ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ምኞታችሁ እንዳያታልላችሁ” ወይም “ራሳችሁን እንዳታታልሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ትመለሱና ሌሎች አማልክትን ታመልካላችሁ

እግዚአብሔርን መተውና ሌሎች አማልክትን ማምለክ ሰው በአካሉ ከእግዚአብሔር ተለይቶ በሌላ አቅጣጫ እንደሚሄድ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ሌሎች አማልክትን ማምለክ ትጀምራላችሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የእግዚአብሔር ቁጣ በእናንተ ላይ እንዳይነድ

የእግዚአብሔር መቆጣት መንደድ እንደ ጀመረ እሳት ተደርጎ ተነግሯል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስለዚህ እግዚአብሔር በእናንተ ላይ እንዳይቆጣ” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ምድር ፍሬዋን እንዳትሰጥና ዝናብን እንዳይሰጡ ሰማያትን እንዳይዘጋቸው

እግዚአብሔር ዝናብ ከሰማይ እንዳይወርድ ማድረጉ እርሱ ሰማይን እንደሚዘጋ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “በምድሪቱ ላይ ሰብል እንዳይበቅል ዝናብ ከሰማይ እንዳይዘንብ እንዳያደርግ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 11:18

እነዚህን ቃሎቼን በልባችሁና በነፍሳችሁ ውስጥ አኑሩ

ሙሴ የሚያዝዘውን ዘወትር የሚያስብና የሚያመዛዝን ሰው ልቡና ነፍሱ መያዣ ዕቃ እንደሆኑና የሙሴ ቃላት መያዣውን እንደሚሞላ አንዳች ይዘት ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ አ.ት፡ “የምነግራችሁን እነዚህን ቃላት ለማስታወስ በጣም ተጠንቀቁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እነዚህን ቃሎቼን

“የሰጠኋችሁን እነዚህን ትዕዛዛት”

ልባችሁንና ነፍሳችሁን

እዚህ ጋ “ልብ” እና “ነፍስ” የሚወክሉት የአንድን ሰው አዕምሮ ወይም አሳብ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እሰሯቸው

“እነዚህን ቃላት እሰሯቸው”። ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር በብራና ላይ የሚጽፍን፣ ብራናውን በትንሽ ኪስ መሰል ማስቀመጫ የሚከተውንና የሚያስረውን ሰው ይወክላል። ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር በሌላ መልኩ ሕዝቡ የሙሴን ትዕዛዛት ለመታዘዝ መጠንቀቅ አለበት የሚል ትርጉም ያለው ዘይቤአዊ አነጋገር ሊሆን ይችላል። ተመሳሳዮቹን ሐረጎች በዘዳግም 6፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእጅህ ላይ እንደ ምልክት

“ሕጌን እንድታስታውስ እንደሚያደርግህ አንዳች ነገር”

በዐይኖችህ መካከል እንደ ክታብ ይሁኑልህ

“ቃሎቼ በዐይኖችህ መካከል እንደ ክታብ ይሆኑልህ”። ይህ የሙሴን ቃላት በብራና ላይ የሚጽፍ፣ ብራናውን በትንሽ ኪስ መሰል ማስቀመጫ የሚከትና በዐይኖቹ መካከል የሚያስርን ሰው የሚወክል ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር በሌላ መልኩ ያ ሰው ሙሴ የሚያዘውን ትዕዛዝ ሁሉ ለመታዘዝ መጠንቀቅ አለበት የሚል ትርጉም ያለው ዘይቤአዊ አነጋገር ሊሆን ይችላል። በዘዳግም 6፡8 ላይ ተመሳሳዮቹን ሐረጎች እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ክታቦች

አንድ ሰው በግምባሩ ላይ የሚያስራቸው ጌጣ ጌጦች

በቤትህ ስትቀመጥ፣ በመንገድ ስትሄድ፣ ስትተኛና ስትነሣ

“በቤትህ” እና “በመንገድ” የሚሉትን የተለያዩ ቦታዎች መጠቀምና ተቃራኒዎቹ “ስትተኛ” እና “ስትነሣ” ሁልጊዜ በሁሉ ቦታ ማለትን ይወክላሉ። የእስራኤል ሕዝቦች በየትኛውም ጊዜና በየትኛውም ቦታ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ማጥናትና ለልጆቻቸው ማስተማር ነበረባቸው። (See: Merism)

Deuteronomy 11:20

በቤትህ መቃኖችና በከተማህ መግቢያ በሮች ላይ ጻፋቸው

እነዚህን ቃላት በዘዳግም 6፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

የአንተ ዕድሜና የልጆችህ ዕድሜ እንዲረዝም

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር አንተንና ልጆችህን ረጅም ዕድሜ እንድትኖሩ እንዲያደርጋችሁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ለአባቶችህ

ይህ አብርሃምን፣ ይስሐቅንና ያዕቆብን ያመለክታል።

ከምድር በላይ እስከ ሰማይ የሚደርስ ዕድሜ ይሰጣቸው ዘንድ

ሕዝቡ በምድሪቱ የሚኖሩበት ዘመን ሰማይ ከምድር በላይ ለምን ያህል ጊዜ ከመቆየቱ ጋር ተነጻጽሯል። ይህ “ለዘላለም” ብሎ የመናገር መንገድ ነው። አ.ት፡ “ለዘላለም የእነርሱ እንዲሆን ሊሰጣቸው” ወይም “በዚያ ለዘላለም እንዲኖሩ ለመፍቀድ” (See: Simile)

Deuteronomy 11:22

ታደርጓቸው ዘንድ እኔ የማዛችሁን እነዚህን ትዕዛዛት ሁሉ በትጋት ብትጠብቁ

“ያዘዝኳችሁን ሁሉ ለመፈጸም ብትጠነቀቁ”

በመንገዶቹ ሁሉ ትሄዱ

አንድ ሰው እንዴት መኖርና ማድረግ እንዳለበት እግዚአብሔር መፈለጉ እንደ እግዚአብሔር መንገድ ወይም ጎዳና ተደርጎ ተነግሯል። አንድ ሰው እግዚአብሔርን ሲታዘዝ በእግዚአብሔር መንገድ ወይም ጎዳና እንደሄደ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእርሱ ጋር ትጣበቁ

ከእግዚአብሔር ጋር የመልካም ግንኙነት መኖርና ሙሉ በሙሉ በእርሱ ላይ መታመን አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር እንደሚጣበቅ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “በእርሱ ለመታመን” ወይም “ከእርሱ ጋር መልካም ግንኙነት እንዲኖር”። ተመሳሳዮቹ ቃላት በዘዳግም 10፡20 ላይ እንዴት እንደተተረጎሙ ተመልከት። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከአንተ በፊት የነበሩትን እነዚህን ሀገሮች ሁሉ፣ ሀገሮችን ታስለቅቃላችሁ

እዚህ ጋ “ሀገሮች” የሚወክሉት ቀድሞ በከነዓን ይኖሩ የነበሩትን የሕዝብ ወገኖች ነው። አ.ት፡ “ከእናንተ በፊት የነበሩትን እነዚህን የሕዝብ ወገኖች ሁሉ፣ ከሕዝብ ወገኖች ምድሪቱን ትወስዳላችሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእናንተ ይልቅ ብዙና ኃያላን የሆኑትን

የእስራኤል ሰራዊት በከነዓን ከሚኖሩት የሕዝብ ወገኖች ይልቅ ጥቂትና ደካማ ቢሆኑም እንኳን የእስራኤል ሕዝብ ድል እንዲያደርጉ እግዚአብሔር ያስችላቸዋል።

Deuteronomy 11:24

የእግራችሁ ጫማ የሚረግጠውን ስፍራ ሁሉ

እዚህ ጋ “የእግራችሁ ጫማ” የሚወክለው የሰውን ሁለንተና ነው። አ.ት፡ “የምትሄዱበት ስፍራ ሁሉ” (See: Synec- doche)

ከወንዝ፣ የኤፍራጥስ ወንዝ

“ከኤፍራጥስ ወንዝ”

በፊታችሁ መቆም የሚችል ሰው አይኖርም

“በፊታችሁ መቆም” የሚለው ሐረግ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ማንም ሊያስቆማችሁ አይችልም” ወይም “ማንም ሊቃወማችሁ አይችልም”

አምላካችሁ እግዚአብሔር ማስፈራታችሁንና ማስደንገጣችሁን በምትረግጡት ምድር ሁሉ ላይ ያኖራል

እግዚአብሔር ሕዝቡ በጣም እንዲፈሩ ማድረጉ ፍርሐትና ድንጋጤን እርሱ እንደ ዕቃ በሕዝቡ ላይ እንደሚያኖራቸው በመሰለ መልኩ ተነግሯል። አ.ት፡ “አምላካችሁ እግዚአብሔር በምትሄዱበት ስፍራ ሁሉ ሕዝቡ እንዲፈሯችሁ ያደርጋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ማስፈራታችሁና ማስደንገጣችሁ

“ፍርሐት” እና “ድንጋጤ” የሚሉት ቃላት ትርጉማቸው ተመሳሳይ ሲሆን የፍርሐቱ መጠን ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “ከእናንተ የተነሣ ከባድ ፍርሐት” (See: Doublet)

በምትረግጡት ምድር ሁሉ ላይ

እዚህ ጋ “ምድሪቱ” የሚለው በምድሪቱ ላይ የሚኖሩትን ሰዎች በሙሉ የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “በምትሄዱበት ስፍራ ሁሉ በሚኖሩ ሰዎች ሁሉ ላይ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 11:26

ተመልከቱ

“ልብ በሉ”

ዛሬ በረከትን እና መርገምን በፊታችሁ አኖራለሁ

እግዚአብሔር እንዲባርካቸው ወይም እንዲረግማቸው ይፈልጉ እንደሆነ ሕዝቡ እንዲመርጡ መፍቀዱ በረከትና መርገም ሙሴ በፊታቸው እንደሚያስቀምጣቸው ቁሶች ተደርገው ተነግሮላቸዋል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እንዲባርካችሁ ወይም እንዲረግማችሁ ዛሬ መምረጥ አለባችሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በረከቱ -- መርገሙ --

የነገር ስም የሆነው “በረከት” እና “መርገም” በግሥነት ሊተረጎሙ ይችላሉ። አ.ት፡ “… ካደረጋችሁ እግዚአብሔር ይባርካችኋል፣ … እግዚአብሔር ይረግማችኋል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ሌሎች አማልክትን ለመከተል እኔ ዛሬ ከማዛችሁ መንገድ ፈቀቅ ብትሉ ግን

ሙሴ ለሕዝቡ የሚነግራቸው የእግዚአብሔር ትዕዛዝ እንደ እግዚአብሔር መንገድ ወይም ጎዳና ሆነው ተነግረዋል። ለእግዚአብሔር ትዕዛዝ ያለመታዘዝ ሌሎች አማልክቶችን ለመከተል በሌላ አቅጣጫ ለመመለስ ከእግዚአብሔር በአካል እንደተለዩ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ሌሎች አማልክትን ለማምለክ ዛሬ እኔ የማዛችሁን ትዕዛዝ እምቢ ብትሉ ግን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የማታውቃቸውን ሌሎች አማልክት

ይህ የሚያመለክተው ሌሎች የሕዝብ ወገኖች የሚያመልኳቸውን አማልክት ነው። እስራኤላውያን ራሱን ስለገለጠላቸውና ኃይሉን ስለተለማመዱ እግዚአብሔርን ያውቁታል።

Deuteronomy 11:29

በረከቱን በገሪዛን ተራራ ላይ፣ መርገሙን በጌባል ተራራ ላይ ታስቀምጣላችሁ

በረከቱ እና መርገሙ አንድ ሰው በተራሮች ላይ እንደሚያስቀምጣቸው ቁሶች ተደርገው ተነግሮላቸዋል። አ.ት፡ “ከእናንተ ጥቂቱ በገሪዛን ተራራ አናት ላይ ቆማችሁ እግዚአብሔር እንዲባርካችሁ የሚያስደርገውን ቃል ታውጃላችሁ፣ ሌሎቹ በጌባል ተራራ አናት ላይ በመቆም እግዚአብሔር እንዲረግማችሁ የሚያስደርገውን ቃል ያውጃሉ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ገሪዛን ተራራ -- ጌባል ተራራ

እነዚህ ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምዕራብ የሚገኙ ተራሮች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በሞሬ --- ከዮርዳኖስ ማዶ የሚገኙ አይደሉም?

እስራኤላውያን የሚገኙት ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ ነው። ሙሴ እነዚህ ተራሮች የሚገኙባቸውን ስፍራዎች ለማስታወስ በጥያቄ መልክ ያቀርባል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ተደርጎ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እንደምታውቁት ሞሬ የሚገኘው ከዮርዳኖስ ማዶ ነው” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ከዮርዳኖስ ማዶ

“ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምዕራብ”

ከምዕራቡ መንገድ በስተምዕራብ

“በምስራቅ”

በጌልገላ ትይዩ

“ጌልገላ አጠገብ” ይህ ምናልባት ኢያሪኮ ከተማ አጠገብ ያለው ስፍራ ላይሆን ይችላል። ምናልባት ሙሴ ሴኬም አቅራቢያ ያለውን ስፍራ እያመለከተ ይሆናል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የሞሬ በሉጥ ዛፎች

እነዚህ በጌልገላ አቅራቢያ የሚገኙ የተቀደሱ ዛፎች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 11:31

ሥርዓቶችና ሕግጋት ሁሉ

እነዚህ ሙሴ በዘዳግም 12፡26 የሚሰጣቸው ሥርዓቶችና ሕግጋት ናቸው።

እኔ ዛሬ በፊታችሁ ያስቀመጥኋቸው

እነዚህ አዲስ ናቸው ማለት አይደለም። ሙሴ ከ40 ዓመታት በፊት የሰጣቸውን ሥርዓቶችና ሕግጋት እየከለሰላቸው ነው።

በፊታችሁ ያስቀመጥኋቸው

ሙሴ ለሕዝቡ የሚነግራቸው ሥርዓቶችና ሕግጋት በሕዝቡ ፊት እንደሚያስቀምጣችው ቁሶች ተደርጎ ተነግሮላቸዋል። አ.ት፡ “እኔ የምሰጣችሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 12

1 የአባቶቻችሁ አምላክ እግዚአብሔር እንድትወርሱ በሚሰጣችሁ ምድር፥ ሁልጊዜ በምድር እያላችሁ የምትጠብቁአችሁ ሥርዓትና ድንጋጌዎች እነዚህ ናቸው። 2 እናንተ የምትወርሱአቸው አሕዛብ አማልክታቸውን ያመለኩባቸውን በረጅም ተራሮች በኮረብቶችም ከለምለምም ዛፍ በታች ያለውን ስፍራ ሁሉ ፈጽማችሁ አጥፉአቸው። 3 መሠዊያቸውንም አፍርሱ፥ ሐውልቶቻቸውንም ሰባብሩ፥የማልመኪያ ዐፀዶቻችቸውንም በእሳት አቃጥሉ፥የአማልክታቸውንም የተቀረጹ ምስሎች ቆራርጡአቸው፥ ከዚያም ስፍራ ስማቸውን አጥፉ። 4 እግዚአብሔር አምላካችሁን እንዲህ ባለ ሁኔታ አታምልኩ። 5 ነገር ግን እግዚአብሔር አምላካችሁ ከነገዶቻችሁ ሁሉ ስሙን በዚያ ያኖር ዘንድ ወደዚያ ወደ መረጠው ስፍራ ትመጣላችሁ፥ ማደሪያውንም ትሻላችሁ። 6 ወደዚያም የሚቃጠለውን መሥዋዕታችሁን፥ ሌላም መሥዋዕታችሁንም፥ አሥራታችሁንም፥ በእጃችሁም ያነሣችሁትን ቁርባን፥ ስእለታችሁንም በፈቃዳችሁ የምታቀርቡትን፥ የላማችሁንና የበጋችሁንም በኩራት ውሰዱ። 7 በዚያም በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ብሉ፥ እጃችሁንም በምትዘረጉበት እግዚአብሔር አምላካችሁ በባረካችሁ ነገር ሁሉ እናንተና ቤተ ሰባችሁ ደስ ይበላችሁ። 8 ሰው ሁሉ በፊቱ መልካም መስሎ የታየውን፥ እኛ በዚህ ዛሬ የምናደርገውን ሁሉ አታደርጉም፥ 9 እግዚአብሔር አምላካችሁ ወደሚሰጣችሁ ዕረፍትና ርስት እስከ ዛሬ ድረስ አልገባችሁምና። 10 ነገር ግን ዮርዳኖስን በተሻገራችሁ ጊዜ እግዚአብሔር አምላካችሁም በሚያወርሳችሁ ምድር በተቀመጣችሁ ጊዜ ያለ ፍርሃትም እንድትኖሩ፥ ከከበቡአችሁ ጠላቶች ሁሉ ዕረፍት በሰጣችሁ ጊዜ በዚያ ጊዜ 11 እግዚአብሔር አምላካችሁ ፥ ስሙ ይጠራበት ዘንድ ወደዚያ ወደ መረጠው ስፍራ እኔ ያዘዝኋችሁን ሁሉ የሚቃጠለውን መሥዋዕታችሁን፥ ሌላም መሥዋዕታችሁን አሥራታችሁንም፥ በእጃችሁ ያነሣችሁትንም ቁርባን፥ ለእግዚአብሔርም ተስላችሁ የመረጣችሁትን ስእልታችሁን ሁሉ ውሰዱ። 12 እናንተም፥ወንዶች ልጆቻችሁና ሴቶች ልጆቻችሁ፥ አገልጋዮቻችሁና የቤት አገልጋዮቻችሁ፥ ከእናንተ ጋር ክፍልና ርስት ስለሌለው በደጆቻችሁ የተቀመጠው ሌዋዊም፥ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት ደስ ይበላችሁ። 13 የሚቃጠለውን መሥዋዕታችሁን በሚታያችሁ ስፍራ ሁሉ እንዳታቀርቡ ተጠንቀቁ። 14 ነገር ግን እግዚአብሔር ከነገዶቻችሁ ከአንዱ ዘንድ በመረጠው ስፍራ በዚያ የሚቃጠለውን መሥዋዕታችሁን አቅርቡ፥ በዚያም የማዝዛችሁን ሁሉ አድርጉ። 15 ይሁን እንጂ እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደሰጣችሁ በረከት ሰውነታችሁ እንደ ፈቀደ በደጆቻችሁ ሁሉ ውስጥ አርዳችሁ ብሉ፤ንጹሕም ያልሆነ ሰው እንደ ሚቋና እንደ ዋላ ያለውን ይብላው። 16 ደሙን ግን እንደ ውኃ በምድር ላይ ያፍስሰው፤ ደሙን አትብሉ። 17 የእህላችሁን፥ የወይናችሁን፥ የጠጃችሁን የዘይታችሁንም፥ አሥራት፥ የላማችሁንና የበጋችሁንም በኩራት የተሳላችሁትንም ስእለት ሁሉ በፈቃዳችሁም ያቀረባችሁትን፥ በእጃችሁም ያነሣችሁትን ቁርባን በደጆቻችሁ መብላት አትችሉም። 18 በዚህ ፈንታ እናንተ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም አገልጋዮቻችሁና የቤት አገልጋዮቻችሁ፥በአገራችሁ ደጅ ያለው ሌዋዊ እግዚአብሔር አምላካችሁ በመረጠው ስፍራ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ብሉት፥ እጃችሁንም በምትዘረጉባችሁ ነገር ሁሉ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ደስ ይበላችሁ። 19 በምድራችሁ ላይ በምትኖሩባት ዘመን ሁሉ ሌዋዊውን ቸል እንዳትሉ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። 20 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ነገራችሁ አገራችሁን ባሰፋ ጊዜ፥ ሰውነታችሁም ሥጋ መብላት ስለ ወደደ፦ ሥጋ እንብላ፥ ስትሉ እንደ ሰውነታችሁ ፈቃድ ሥጋን ብሉ። 21 እግዚአብሔር አምላካችሁ በዚያ ስሙን ያኖር ዘንድ የመረጠው ስፍራ ከእናንተ ሩቅ ቢሆንም እግዚአብሔር ከሰጣችሁ ከላምና ከበግ መንጋችሁ እንዳዛዝኋችሁ እረዱ፥ እንደ ሰውነታችሁም ፈቃድ ሁሉ በአገራችሁ ደጅ ብሉ። 22 ሚዳቋና ዋላ እንደሚበሉ እንዲሁ ብሉ፥ ንጹሕ ሰው ንጹሕ ያልሆነም ይብለው። 23 ደሙ ሕይወት ነውና፥ ነፍሱንም ከሥጋው ጋር መብላት አይገባችሁምና፥ ደሙን እንዳትበሉ ተጠንቀቁ። 24 በምድር ላይ እንደ ውኃ አፍስሱት እንጂ አትብሉ። 25 በእግዚአብሔር ፊት መልካም የሆነውን ነገር ስታደርጉ ለእናንተ፥ ከእናንተም በኋላ ለልጆቻችሁ መልካም እንዲሆንላችሁ አትብሉ። 26 ነገር ግን የተቀደሰውን ነገራችሁን ስእለታችሁንም ይዛችሁ እግዚአብሔር ወደ መረጠው ስፍራ ሂዱ። 27 የሚቃጠለውንም መሥዋዕታችሁን ሥጋውንና ደሙን በአምላካችሁ በእግዚአብሔር መሠዊያ ላይ አቅርቡ፤ የመሥዋዕታችሁም ደም በእግዚአብሔር በአምላካችሁ መሠዊያ ላይ ይፍሰስ፥ ሥጋውንም ብሉ። 28 በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት መልካምና ቅን የሆነውን ነገር ስታደርጉ ለእናንተ፥ ከእናንተም በኋላ ለልጆቻችሁ ለዘላለም መልካም ይሆንላችሁ ዘንድ እኔ የማዝዛችሁን እነዚህን ቃሎች ሁሉ ሰምታችሁ ጠብቁ። 29 እግዚአብሔር አምላካችሁ ትወርሱአቸው ዘንድ የምትሄዱባቸውን አሕዛብን ፊታችሁ ባጠፋ ጊዜ፥ እናንተም በወረሳችሁ ጊዜ፥ በምድራቸውም በተቀመጣችሁ ጊዜ፥ 30 ከፊታችሁ ከጠፉ በኋላ እነርሱን ለመከተል እንዳትጠመዱ፦ እነዚህ አሕዛብ አማልክታቸውን የሚያመልኩት እንዴት ነው? እንዲሁ ደግሞ እኔም አደርጋለሁ ብላችሁ ስለ አማልክታቸው እንዳትጠይቁ ተጠንቀቁ። 31 እግዚአብሔር የሚጠላውን ርኩሰት ሁሉ እነዚህን ለአማልክታቸው አድርገዋል፥ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸውንም ለአማልክታቸው በእሳት አቃጥሎአቸዋል፥ እናንተም ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ እንዲሁ አታድርጉ። 32 እኔ የማዝዛችሁን ነገር ሁሉ ታደርጉ ዘንድ ጠብቁ፤ ምንም በእርሱ ላይ አትጨምሩ ከእርሱም ምንም አታጉድሉ።



Deuteronomy 12:1

የምትጠብቃቸው

“መታዘዝ አለባችሁ”

በምድር ላይ በምትኖሩበት ዘመን ሁሉ

“በምድር ላይ በምትኖሩበት” የሚለው ሐረግ አንድ ሰው በሕይወት እስካለ ደረስ የሚል የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በሕይወት እስካላችሁ ድረስ” (የአነጋገርዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ፈጽማችሁ አጥፉ

“ማጥፋት አለባችሁ”

የምታስለቅቋቸው ሕዝቦች

እዚህ ጋ “ሕዝቦች” የሚወክሉት በከነዓን የሚኖሩትን የሕዝብ ወገኖች ነው። አ.ት፡ “መሬታቸውን የምትወስዱባቸው የሕዝብ ወገኖች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:3

መሠዊያዎቻቸውን ማፍረስ አለባችሁ

“የእነዚያን ሕዝቦች መሠዊያ ማፈራረስ አለባችሁ” ወይም “የእነዚያን ሕዝቦች መሠዊያዎች ማጥፋት አለባችሁ”

ከስክሳችሁ ጣሉ

“ሰባብራችሁ ጣሉ” ወይም “ብትንትናቸውን አውጡ”

ስማቸውን አጥፉ

እዚህ ጋ “ስማቸውን” የሚወክለው “መታሰቢያቸውን” ነው። አ.ት፡ “ማንም እንዳያስታውሳቸው ፈጽማችሁ አጥፏቸው” ወይም “እነዚህን ሐሰተና አማልክት የሚወክል የትኛውንም ነገር አጥፉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከዚያ ስፍራ

ይህ ሕዝቦች አማልክቶታቸውን የሚያመልኩባቸውን እያንዳንዱን ስፍራ ያመለክታል።

አምላካችሁን እግዚአብሔርን በዚያ መልኩ አታምልኩ

“እነዚያ ሕዝቦች አማልክቶቻቸውን እንዳመለኩ አምላካችሁን እግዚአብሔርን ማምለክ የለባችሁም”

Deuteronomy 12:5

አምላካችሁ እግዚአብሔር ስሙን ሊያስቀምጥበት ከነገዶቻችሁ ሁሉ የሚመርጠው ስፍራ

እዚህ ጋ “ስሙን” የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ራሱን ነው። እግዚአብሔር የሚኖርበትን አንድ ቦታ ይመርጣል፣ ሰዎች እርሱን ለማምለክ ወደዚያ ይመጣሉ። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መሄድ የሚኖርባችሁ ወደዚያ ነው

እግዚአብሔር ወደሚወስነው ስፍራ ለማምለክ ይሄዳሉ

በእጃችሁ የምታቀርቡት ስጦታ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ሙሉ ሰውነትን ነው። አ.ት፡ “የምታቀርቡት ስጦታ” (See: Synecdoche)

የስእለቶቻችሁንና የፈቃደኝነት ስጦታዎቻችሁን

“ስእለታችሁን የምትፈጽሙበትን ስጦታዎቻችሁን፣ የበጎ ፈቃድ ስጦታዎቻችሁን”። እነዚህ የስጦታ ዓይነቶች ናቸው።

ከቀንድ ከብቶቻችሁና ከበግና ከፍየል መንጋዎቻችሁ በኩራቱን

ሕዝቡ ከእያንዳንዱ የቤት እንስሳው በመጀመሪያ የሚወለደውን ወንድ እንዲሰጡት እግዚአብሔር ይፈልጋል

Deuteronomy 12:7

በዚያ ነው

ይህ የሚያመለክተው የእስራኤል ልጆች እንዲያመልኩበት እግዚአብሔር የሚመርጥላቸውን ስፍራ ነው።

እጃችሁ በነካው ሁሉ ደስ ይበላችሁ

እዚህ ጋ “እጃችሁ በነካው” የሚወክለው ሙሉውን ሰውና እርሱ የሠራውን ነው። አ.ት፡ “በሠራችሁት ሥራ ሁሉ ደስ ይበላችሁ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 12:8

ዛሬ እዚህ የምናደርጋቸውን ነገሮች ሁሉ ማድረግ የለባችሁም

“ዛሬ እዚህ እንደምናደርገው ማድረግ የለባችሁም”። ይህ ማለት በዚያ ወቅት ከሚያመልኩበት በተለየ ሁኔታ በተስፋይቱ ምድር ማምለክ ይኖርባቸዋል።

አሁን እያንዳንዱ የሚያደርገው በዐይኑ መልካም መስሎ የታየውን ነው

ዐይን ማየትን፣ ማየትም ማሰብን ወይም መወሰንን ይወክላል። አ.ት፡ “እያንዳንዱ የሚያደርገው ልክ ነው ብሎ የሚያስበውን ነው” ወይም “አሁን እያንዳንዱ የሚያደርገው ልክ ነው ብሎ የሚወስነውን ነው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወደ ማረፊያ

“ማረፊያ” የሚለው የነገር ስም እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ወደምታርፉበት ምድር” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

አምላካችሁ እግዚአብሔር ወደሚሰጣችሁ ርስት

እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ የሚሰጣቸው ምድር አባት ለልጆቹ እንደሚተውላቸው ርስት ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “አምላካችሁ እግዚአብሔር እንደ ቋሚ ንብረት አድርጎ ወደሚሰጣችሁ ምድር” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:10

በምድሪቱ ስትኖሩ

ይህ የሚያመለክተው የከነዓንን ምድር ነው።

አማላካችሁ እግዚአብሔር እንድትወርሷት በሚያደርጋችሁ ምድር ላይ

እግዚአብሔር የከነዓንን ምድር ለእስራኤል ሕዝብ መስጠቱ እርሱ ለልጆቹ ርስት እንደሚሰጣቸው አባት ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በዙሪያችሁ ካሉ ከጠላቶቻችሁ ሁሉ ያሳርፋችኋል

“በዙሪያችሁ ካሉ ከጠላቶቻችሁ ሁሉ ሰላምን ይሰጣችኋል”

አምላካችሁ እግዚአብሔር ስሙ በዚያ እንዲቀመጥ በሚመርጠው ስፍራ ላይ

እዚህ ጋ “ስም” የሚወክለው እግዚአብሔርን ራሱን ነው። አ.ት፡ “አምላካችሁ እግዚአብሔር ለመኖር በሚመርጠው ስፍራ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእጃችሁ የምታቀርቡት ስጦታ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ሙሉውን ሰው። አ.ት፡ “የምታቀርቡት ስጦታ” (See: Synecdoche)

ስለ ስእለቶቻችሁ የተመረጡትን ስጦታዎቻችሁን በሙሉ

“ስእለታችሁን ለመፈጸም የምታቀርቧቸውን የበጎ ፈቃድ ስጦታዎቻችሁን በሙሉ”

Deuteronomy 12:12

በእግዚአብሔር ፊት ደስ ይበላችሁ

“በእግዚአብሔር ሀልዎት ደስ ይበላችሁ”

በበራችሁ የሚኖሩ ሌዋውያን

እዚህ ጋ “በሮች” የሚያመለክተው ከተማውን ራሱን ነው። አ.ት፡ “በከተማችሁ ውስጥ የሚኖረው ሌዋዊ” ወይም “ከእናንተ ጋር የሚኖረው ሌዋዊ” (See: Synecdoche)

በመካከላችሁ ምንም ድርሻ ወይም ርስት ስለሌለው

እግዚአብሔር ለሌዋውያን ምንም መሬት ያለመስጠቱ እውነታ ለልጆቹ ርስት እንዳልሰጣቸው አባት ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ምንም ድርሻ የለውም

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚያመለክተው ሌዊን ነው። ሌዊ ተወላጆቹን በሙሉ ይወክላል። አ.ት፡ “ምንም ድርሻ የላቸውም” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:13

ለራሳችሁ ትኩረት ስጡ

“ተጠንቀቁ”

በምታዩት ስፍራ ሁሉ

“ደስ በሚያሰኛችሁ ስፍራ ሁሉ” ወይም “በምትፈልጉት ስፍራ ሁሉ”

ነገር ግን እግዚአብሕር በሚመርጠው ስፍራ ነው

የሚቃጠል ስጦታ መቅረብ ያለበት በመገናኛው ድንኳን ነው። የመገናኛው ድንኳን የት መደረግ እንዳለበት እግዚአብሔር ራሱ ይመርጣል።

Deuteronomy 12:15

ይሁን እንጂ፣ በየበሮቻችሁ ውስጥ እንስሶችን አርዳችሁ መብላት ትችላላችሁ

ሕዝቡ ለመሥዋዕት እንስሶችን ማረድ የሚችለው እግዚአብሔር በሚመርጠው ስፍራ ብቻ ነው። ለምግብ የሚሆኑ እንስሶችን በፈለጉበት ሁሉ ማረድ ይችላሉ። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በይበልጥ ግልጽ መደረግ ይችላል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information

በየበሮቻችሁ ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮች” ከተማውን በሙሉ ይወክላሉ። አ.ት፡ “በከተማችሁ ውስጥ” ወይም “በቤታችሁ” (See: Synecdoche)

ንጹሕ ያልሆኑ ሰዎች

ለእግዚአብሔር አገልግሎት ተቀባይነት የሌለው ሰው በአካሉ ንጹሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕ የሆኑ ሰዎች

ለእግዚአብሔር አገልግሎት ተቀባይነት ያለው ሰው በአካሉ ንጹሕ እንደሆነ ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሚዳቋና ድኩላ

እነዚህ በፍጥነት መሮጥ የሚያስችል ቀጭንና ረጅም እግሮች ያሏቸው የዱር እንስሶች ናቸው። አ.ት፡ “አጋዘንና ድኩላ” (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

ነገር ግን ደሙን አትብሉ

ደም ሕይወትን ስለሚወክል ሕዝቡ ደሙን ከምግባቸው ጋር እንዲበሉት እግዚአብሔር አልፈቀደላቸውም። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 12:17

በበሮችህ ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክሉት መላውን ከተማ ይወክላሉ። አ.ት፡ “በከተማህ ውስጥ” ወይም “በቤትህ ውስጥ” (See: Synecdoche)

በእጅህ የምታቀርበውን ስጦታ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ሙሉውን ሰው። አ.ት፡ “ለእግዚአብሔር የምታቀርበውን የትኛውንም ስጦታ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 12:18

ትበሉታላችሁ

“ስጦታዎቻችሁን ትበላላችሁ”

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ሀልዎት”

በበሮቻችሁ ውስጥ ያሉ ሌዋውያን

እዚህ ጋ “በር” የሚወክለውን መላውን ከተማ ነው። አ.ት፡ “በከተማችሁ ውስጥ የሚኖር ሌዋዊ ሁሉ” (See: Synecdoche)

እጅህን የምታኖርበት የትኛውም ነገር

እዚህ ጋ “እጅህን የምታኖርበት” የሚወክለው ሙሉውን ሰውና እርሱ የሚሠራውን ነው። አ.ት፡ “ስላሠራኸው ሥራ ሁሉ ደስ ይበልህ” (See: Synecdoche)

ለራስህ ትኩረት ስጥ

“ተጠንቀቅ”

እንዳትረሳ

ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በሚገባ ጠብቀው” (ድርብ አሉታ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:21

ስሙን ለማስቀመጥ የመረጠው

እዚህ ጋ “ስም” የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ራሱን ነው። እርሱ የሚኖርበትንና ሕዝቡ እርሱን ለማምለክ የሚመጣበትን ስፍራ እግዚአብሔር ይመርጣል። አ.ት፡ “መኖሪያውን ይመርጣል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በበሮችህ ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክሉት መላውን ከተማውን ነው። አ.ት፡ “በከተማህ ውስጥ” ወይም “በማኅበረሰብህ መካከል” (See: Synecdoche)

ነፍስህ እንደ ተመኘች

እዚህ ጋ “ነፍስ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “እንደምትመኘው” (See: Synecdoche)

ሚዳቋና ድኩላ የሚበሉ እንደሆኑ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ልክ ሚዳቋውን እና ድኩላውን እንደምትበላ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሚዳቋና ድኩላውን

እነዚህ በፍጥነት መሮጥ የሚችሉ ቀጭንና ረጅም እግሮች ያሏቸው የዱር እንስሶች ናቸው። እነዚህን በዘዳግም 12፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ንጹሕ ያልሆኑ ሰዎች

ለእግዚአብሔር አገልግሎት ተቀባይነት የሌለው ሰው በአካሉ ንጹሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕ የሆኑ ሰዎች

ለእግዚአብሔር አገልግሎት ተቀባይነት ያለው ሰው በአካሉ ንጹሕ እንደሆነ ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:23

ደሙ ሕይወቱ ነው

እዚህ ጋ ደም ሕይወትን የሚያቆይበት መንገድ ደም ራሱ ሕይወት እንደሆነ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ደሙ ሕይወትን ያቆያል” ወይም “ሰዎችና እንስሳት በሕይወት እንዲኖሩ የሚያደርጋቸው ደም ነው።” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሕይወቱን ከሥጋው ጋር አትብላው

እዚህ ጋ፣ “ሕይወት” የሚለው ቃል የሚወክለው ሕይወትን የሚያቆየውን ደሙን ነው። አ.ት፡ “ሕይወትን የሚያቆየውን ከሥጋ ጋር አትብላው” ወይም “ሕይወትን የሚያቆየውን ደም ከሥጋ ጋር አትብላ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእግዚአብሔር ዐይን ትክክል የሆነውን

ዐይን ማየትን ይወክላል፣ ማየትም ማሰብን ወይም መወሰንን ይወክላል። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ውሳኔ ትክክል የሆነው” ወይም “እግዚአብሔር ትክክል ነው የሚለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:26

ስለ ስእለቶችህ የምታቀርባቸውን ስጦታዎች

“ስእለቶችህን ለመፈጸም ስጦታዎችን” ወይም “የስእለት ስጦታዎች”

የመሥዋዕትህ ደም መፍሰስ አለበት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ካህኑ የመሥዋዕቱን ደም ያፈሰዋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሥጋውን ትበላለህ

የእግዚአብሔር ሕግ የእንስሳው የትኛው ክፍል የሚቃጠል መሥዋዕት፣ የትኛው ክፍል ለካህኑ እንደሚሆንና የትኛውን ክፍል አቅራቢው መብላት እንዳለበት ግልጽ ያደርጋል። የዚህ መግለቻ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከሥጋው ጥቂቱን ትበላለህ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 12:28

እኔ የማዝህን እነዚህን ቃላት በሙሉ ስማ፣ በጥንቃቄም ጠብቃቸው

“የማዝህን ሁሉ በጥንቃቄ ስማና ታዘዘው”

ለአንተና ከአንተም በኋላ ለልጆችህ መልካም እንዲሆንልህ

እዚህ ጋ “ልጆች” ማለት ተወላጆቻቸው ሁሉ ማለት ነው። አ.ት፡ “አንተና ተወላጆችህ እንድትበለጽጉ” (See: Synecdoche)

መልካምና ትክክለኛውን ነገር በምታደርግበት ጊዜ

“መልካም” እና “ትክክለኛ” የሚሉት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆኑ ትክክለኛ ባህርይ አስፈላጊ በመሆኑ ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “ትክክል የሆነውን በምታደርግበት ጊዜ” (See: Doublet)

በእግዚአብሔር ዐይን መልካምና ትክክል

ዐይን ማየትን ይወክላል፣ ማየትም ማሰብን ወይም መወሰንን ይወክላል። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ውሳኔ መልካምና ትክክል የሆነው” ወይም “እግዚአብሔር መልካምና ትክክል ነው የሚለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:29

ሕዝቦችን ይቆርጣቸዋል

እግዚአብሔር በከነዓን የሚኖሩትን የሕዝብ ወገኖች ማጥፋቱ አንድ ሰው ቁራጭ ጨርቅ ወይም ከዛፍ ላይ ቅርንጫፍን እንደሚቆርጥ እንደሚቆርጣቸው ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሕዝቦች

እዚህ ጋ “ሕዝቦች” የሚወክሉት በከነዓን የሚኖሩትን ሰዎች ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ታስወጧቸዋላችሁ፣ በምታስወጧቸው ጊዜ

“ሁሉንም ነገር በምትወስዱባቸው ጊዜ”

ለራሳችሁ ትኩረት ስጡ

“ተጠንቀቁ”

እነርሱን በመከተል እንዳትጠመዱ -- አማልክታቸውን ለመጠየቅ በመሞከር እንዳትጠመዱ

ስለ ሌሎች አማልክት የሚማርና የሚያመልክ ሰው በአዳኝ ወጥመድ እንደሚያዝ ሆኖ ተነግሮለታል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እንደ እነርሱ አታድርጉ … አማልክታቸውን የመጠየቅ ሙከራ ለማድረግ እንዳትማሩ” (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት))

እነርሱን በመከተል አትጠመዱ

የከነዓን የሕዝብ ወገኖች ጣዖታትን እንደሚያመልኩ እስራኤላውያን ጣዖታትን ማምለካቸው ከሌሎች የሕዝብ ወገኖች በስተኋላ እንደ ተከተሉ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእናንተ አስቀድሞ ከጠፉ በኋላ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በፊታችሁ ካጠፋቸው በኋላ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

‘እነዚህ ሕዝቦች አማልክታቸውን የሚያመልኩት እንዴት ነው? እኔም እንደዚያው አደርጋለሁ’ ብለህ ብትጠይቅ

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ ነው። ቀጥተኛ የሆነው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ተደርጎ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንተም እንደዚያው ልታደርግ እነዚያ የሕዝብ ወገኖች አማልክታቸውን እንዴት እንዳመለኩ ብትጠይቅ” (በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ እና ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 12:31

በእርሱ ላይ አትጨምር፣ ከእርሱም አትቀንስ

ተጨማሪ ሕጎችን መፍጠርም ሆነ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ሕጎች ቸል ማለት አይኖርባቸውም።


Chapter 13

1 በመካከላችሁም፦ ነቢይ ወይም ሕልም አላሚ ቢነሣ፥ ምልክት ወይም ተአምራት ቢሰጣችሁ፥ እንደ ነገራችሁም 2 ምልክቱ ወይም ተአምራቱም ቢፈጸም፥ እርሱም፦ የማታውቃቸውን ሌሎች አማልክት ሄደን እንከተል እናምልካቸውም ቢላችሁ፥ 3 እግዚአብሔር አምላካችሁን በፍጹም ልባችሁ፥ በፍጹም ነፍሳችሁ ትወድዱት እንደሆነ ያውቅ ዘንድ እግዚአብሔር አማላካችሁ ሊፈትናችሁ ነውና፥ የዚያን ነቢይ ቃል ወይም ያን ሕልም አላሚ አትስሙ። 4 እግዚአብሔር አምላካችሁን ተከተሉ፥ እርሱንም አክብሩ፥ ትእዛዘትንም ጠብቁ፥ ድምፁንም ስሙ፥ እርሱንም አምልኩት፥ ከእርሱም ጋር ተጣበቁ። 5 ከግብፅ ምድር ካወጣችሁና ከባርነት ቤት ካዳናችሁ ከእግዚአብሔር ከአምላካችሁ ሊያስታችሁ ስለተናገረ ያ ነቢይ ወይም ያ ሕልም አላሚ ይገደል። ያም ነቢይ እግዚአብሔር አምላካችሁ እንድትሄዱበት ካዘዛችሁ መንገድ ሊያወጣችሁ ነው። ስለዚህ ክፉውን ነገር ከመካከላችሁ አርቁ። 6 የእናታችሁ ልጅ፥ ወንድማችሁ ወይም ወንድ ልጃችሁ ወይም ሴት ልጃችሁ ወይም በብብታችሁ ያለች ሚስታሁ ወይም እንደ ነፍሳችሁ የምትቆጥሩት ወዳጃችሁ በስውርም ሊፈትናችሁ፦ ኑ፥ እናንተ ወይም አባቶቻችሁ የማታውቁአችሁን አማልክት ሄደን እናምልክ ብሉአችሁ፥ 7 ከምድር ዳር ጀምሮ እስከ ሌላኛው ምድር ዳር ድረስ ወደ እናንተ የቀረቡት ከእናንተም የራቁት በዙሪያችሁ ያሉ አሕዛብ ከሚያመልኩአቸው አማልክት ቢያስታችሁ እሺ አትበሉ። 8 አትስማሙአቸው፤አትስማቸውም። ዓይናችሁም አይራራላቸው፥ አትምራቸውም፥ አትሸሽጋቸውም። 9 በዚህ ፈንታ ፈጽማችሁ ግደሉአቸው፤ እርሱን ለመግደል የእናንተ እጅ በእርሱ ላይ ይሁን፤ ከዚያም በኋላ የሕዝቡ ሁሉ እጅ በላዩ ይሁን። 10 ከግብፅ ምድር ከባርነት ቤት ካወጣችሁ ከእግዚአብሔር ከአምላካችሁ ሊያርቃችሁ ወድዶአልና፥ እስኪሞት ድረስ በድንጋይ ውገሩት። 11 እስራኤልም ሁሉ ይህን ሰምተው ይፈራሉ፥ በመካከላችሁም እንዲህም ያለ ክፉ ሥራ ለማድረግ አይቀጥሉም። 12 እግዚአብሔር አምልካችሁ ልትኖሩባችሁ በሚሰጣችሁ በአንዲቱ ከተማችሁ እንዲህ ሲባል ብትሰሙ፡- 13 አንዳንድ ክፉ ሰዎች ከእናንተ መካከል ወጥተው፦ የማታውቋቸውን ሌሎችን አማልክት ሄደን እናምልክ ብለው የከተማቸውን ሰዎች አሳቱ፥ ሲሉ ብትሰሙ፤ 14 ታጣራላችሁ፥ ትመረምራላችሁ፥ በሚገባም ትጠይቃላችሁ። እነሆም፥ ይህም ክፉ ነገር በመካከላችሁ እንደ ተደረገ እውነት ሆኖ ቢገኝ። 15 የዚያችን ከተማ ሰዎች በሰይፍ ስለት ፈጽሞ ትመታቸዋላችሁ፤ ከተማይቱን በእርስዋም ያለውን ሁሉ እንስሳውንም በሰይፍ ስለት ታጠፉአቸዋላችሁ። 16 ዕቃዋንም ሁሉ ወደ አደባባይዋ ትሰበስባላችሁ፥ ከተማይቱንም ዕቃዋንም ሁሉ ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ በእሳት ፈጽማችሁ ታቃጥላላችሁ፤ እንደ ገና የማትሠራ ሆና ለዘላለም እንደ ፈረሰች ትቀራለች። 17 ለጥፋት ከተለዩ ነገሮች ምንም እርም ነገር በእጃችሁ አይገኙ። እግዚአብሔር ከቁጣ ትኩሳት ይመለስ ዘንድ፥ ለአባቶቻችሁም እንደማለላቸው ይምራችሁና ይራራላችሁ ዘንድ፥ ያበዛላችሁም ዘንድ ነው። 18 ዛሬ እኔ የማዝዛችሁን ትእዛዘት ሁሉ ትጠብቁ ዘንድ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት ደስ የሚያሰኘውን ታደርጉ ዘንድ የእግዚአብሔር የአምላካችሁን ቃል ስሙ።



Deuteronomy 13:1

በመካከላችሁ ቢነሣ

“በመካከላችሁ ቢመጣ” ወይም “በመካከላችሁ ነኝ ቢል”

የሕልመኛው ሕልሞች

ይህ ከእግዚአብሔር በሕልም መልዕክት የሚቀበል ሰው ነው።

ምልክትን ወይም ድንቅን

እነዚህ ሁለት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆኑ የተለያዩ ተአምራቶችን ያመለክታል። (See: Doublet)

ቢሆን

“ቢከናወን” ወይም “ቢመጣ”

ቢነግርሃና፣ ‘ሌሎች አማልክትን እንከተል፣ የማታውቃቸውን እናምልክ’ ቢልህ አትስማው

ይህ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ተደርጎ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “የማታውቃቸውን ሌሎች አማልክት እንድታመልክና እንድታገለግል ቢነግርህ አትስማው” (ቀጥተና እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

ከሌሎች አማልክት ኋላ እንሂድ

ሌሎች አማልክትን ማምለክ ከሌሎች አማልክት ኋላ መሄድ ወይም መከተል ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ሌሎች አማልክትን እንከተል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከማታውቃቸው ሌሎች አማልክት ኋላ ሂድ

“ከማታውቃቸው አማልክት” የሚለው ሐረግ የሚያመለክተው ሌሎች የሕዝብ ወገኖች የሚያመልኳቸውን አማልክት ነው። ራሱን ስለገለጠላቸውና ኃይሉን ስለተለማመዱት እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ያውቁታል።

የዚያን ነቢይ ወይም ሕልም አላሚ ቃል አትስማ

“ያ ነቢይ የሚለውንም ሆነ ሕልም አላሚው የሚናገረውን አትስማው”

በሙሉ ልብህና በሙሉ ነፍስህ

እዚህ ጋ “ልብ” እና “ነፍስ” የአንድን ሰው ውስጣዊ ማንነት የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። እነዚህ ሁለት ሐረጎች “በፍጹም” ወይም “በቅንነት” የሚል ትርጉም እንዲሰጡ በአንድነት ጥቅም ላይ ውለዋል። ይህንን በዘዳግም 4፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 13:4

አምላካችሁን እግዚአብሔርን ተከተሉት

እግዚአብሔርን መታዘዝና ማምለክ ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ኋላ እንደ ሄዱ ወይም እንደተከተሉት ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን ታዘዙ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ድምፁን ታዘዙ

እዚህ ጋ “ድምፅ” የሚወክለው እግዚአብሔር የሚናገረውን ነው። አ.ት፡ “እርሱ የሚለውን ታዘዙ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእርሱ ጋር ተጣበቁ

ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት መኖሩና ሙሉ በሙሉ በእርሱ ላይ መታመን ሰው ከእግዚአብሔር ጋር እንደሚጣበቅ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “በእርሱ ተማመን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ይገደል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “መግደል አለብህ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

አመፅን ተናግሯልና

የነገር ስም የሆነው “አመፅ” እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እንድታምፅ ሊያደርግህ ሞክሯል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ከባርነት ቤት የተቤዠህን

እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ባሪያ ከነበሩበት ከግብፅ ማዳኑ ሕዝቡን ከባርነት ለመቤዠት ገንዘብ እንደከፈለ በሚመስል መልኩ ተነግሯል። አ.ት፡ “ ባሪያዎች ከነበራችሁበት ስፍራ ያዳናችሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የባርነት ቤት

እዚህ ጋ “የባርነት ቤት” የእግዚአብሔር ሕዝብ ባሪያዎች የነበሩበትን ግብፅን ይወክላል። አ.ት፡ “ባሪያዎች የነበራችሁበት ግብፅ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አምላካችሁ እግዚአብሔር እንድትሄዱበት ካዘዛችሁ መንገድ እንድትወጡ

እግዚአብሔር አንድ ሰው እንዴት መኖር ወይም ማድረግ እንዳለበት የሚፈልግበት ሁኔታ ሕዝቡ እንዲሄዱበት እንደሚፈልገው መንገድ ወይም ጎዳና ሆኖ ተነግሯል። አንድን ሰው እግዚአብሔርን ከመታዘዝ ለማስቆም የሚሞክር በእግዚአብሔር መንገድ ወይም ጎዳና ላይ እንዳይሄድ እንደተከላከል ሆኖ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር ያዘዘውን እንዳትፈጽም የሚያደርግህ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስለዚህ ክፋትን ከመካከላችሁ አርቁ

እዚህ ጋ “ክፋትን” የሚያመለክተው ክፉ ሰውን ወይም ክፉ ባህርይን ነው። ይህ ስማዊ ቅጽል እንደ ቅጽል ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስለዚህ ይህንን ክፉ ነገር የሚያደርገውን ሰው ከእስራኤል ሕዝብ መካከል ማስወገድ አለብህ” ወይም “ስለዚህ ይህንን ክፉ ሰው መግደል አለብህ” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 13:6

በእቅፍህ ያለች ሚስትህ

እቅፍ የሰው ድረት ነው። ይህ የአነጋገር ዘይቤ ወደ ደረቱ አስጠግቶ ይይዛታል፣ ይኸውም ይወዳታል፣ ይንከባከባታል ማለት ነው። አ.ት፡ “የምትወዳት ሚስትህ” ወይም “በፍቅር የምታቅፋት ሚስትህ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እንደ ነፍስህ የሆነ ጓደኛህ

እዚህ ጋ “ነፍስ” የሚወክለው የሰውን ሕይወት ነው። ይህ ማለት ሰውየው ለራሱ ሕይወት የሚገደውን ያህል ስለ ጓደኛው ይገደዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “ውድ ጓደኛህ” ወይም “ራስህን የምትወደውን ያህል የምትወደው ጓደኛህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በምስጢር ሊያስትህ፣ ‘በሌላው የምድር ጫፍ -- እንሂድና እናምልክ’ ቢልህ

ይህ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ወደ ሌላው የምድር ጫፍ ሄደህ እንድታመልክ ሊያሳምንህ በምስጢር ይሞክራል” (ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

በክበብህ ያሉ

“በዙሪያህ ያሉ”

ከአንዱ የምድር ጫፍ እስከ ሌላኛው የምድር ጫፍ

እዚህ ጋ ሁለቱ የምድር ጽንፍ ማጣቀሻዎች “በምድር ላይ በሁሉ ስፍራ” ማለት ነው። አ.ት፡ “በመላው ምድር ላይ” (See: Merism)

Deuteronomy 13:8

እሺ አትበለው

“እርሱ በሚፈልገው አትስማማ”

ዐይንህ አይራራለት

እዚህ ጋ “ዐይንህ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “በርኅራኄ አትመልከተው” ወይም “አትማረው” (See: Synecdoche)

አትተወው ወይም አትደብቀው

“ምህረት ልታሳየው ወይም እርሱ ያደረገውን ከሌሎች ልትደብቅ አይገባም”

እርሱን ለመግደል መጀመሪያ የአንተ እጅ ይሁንበት

ይህ ማለት በበደለኛው ሰው ላይ የመጀመሪያውን ድንጋይ እርሱ መወርወር ነበረበት። “እጅ” የሚለው ቃል የሚወክለው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “በመጀመሪያ እስኪሞት ድረስ የምትመታው አንተ መሆን አለብህ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 13:10

ከእግዚአብሔር ሊያርቅህ ሞክሯል

“ከእግዚአብሔር ሊመልስህ”። አንድ ሰው ሌላውን እግዚአብሔርን ከመታዘዝ ሊገታው መሞከሩ ያንን ሰው በአካሉ እግዚአብሔርን ትቶ እንዲመለስ ለማድረግ እንደሞከረ ተቆጥሮ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን እንዳትታዘዝ ሊያደርግህ ሞክሯል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከባርነት ቤት

እዚህ ጋ፣ “የባርነት ቤት” የሚወክለው የእግዚአብሔር ሕዝብ ባሪያዎች የነበሩበትን ግብፅን ነው። አ.ት፡ “ባሪያዎች ከነበራችሁበት ስፍራ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እስራኤል ሁሉ ይሰሙና ይፈራሉ

ሕዝቡ ስለተገደለው ሰው በሚሰሙበት ጊዜ እርሱ እንዳደረገው ለማድረግ እንደሚፈሩ ያመለክታል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 13:12

አንዳንድ ክፉ ሰዎች ከመካከልህ ሄደው

“ከመካከልህ” የሚለው ሐረግ እነዚህ ክፉ ሰዎች በማኅበረሰቡ መካከል የሚኖሩ እስራኤላውያን ነበሩ ማለት ነው።

የከተማቸውን ነዋሪዎች ሰብስበው፣ ‘ሄደን የማታውቋቸውን አማልክት እናምልክ’ ቢሉ

ይህ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “የማያውቋቸውን አማልክት ሄደው እንዲያመልኩ በከተማቸው የሚኖሩትን አስገድደዋል”። (ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

የከተማቸውን ነዋሪዎች ሰብስበው

አንድ ሰው ሌላውን እግዚአብሔርን እንዳይታዘዝ ቢያደርገው ያ ሰው በአካሉ ከእግዚአብሔር ተለይቶ እንዲመለስ እንዳደረገው ተቆጥሮ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መረጃውን አጣራ፣ ፈትሽ፣ በሚገባ መርምር

እነዚህ ሐረጎች ሁሉ በመሠረቱ የሚሉት አንድ ነገር ነው። ሙሴ በከተማይቱ ስለሆነው ነገር እውነቱን በጥንቃቄ እንዲያጣሩ አጽንዖት እየሰጠ ነው። (See: Doublet)

እንዲህ ያለ አስጸያፊ ነገር በመካከላችሁ ተደርጎ እንደሆን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የከተማይቱ ሰዎች እንዲህ ያለ አስከፊ ነገር አድርገው እንደሆን (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 13:15

በሰይፍ ስለት

እዚህ ጋ “ስለት” የሚወክለው ሙሉውን ሰይፉን ነው። አ.ት፡ በሰይፎቻችሁ” (See: Synecdoche)

ምርኮውን ሁሉ

“ብዝበዛውን ሁሉ”። ይህ ሰራዊት በጦርነት ድል ካደረገ በኋላ የሚሰበስበውን ሀብትና ንብረት ያመለክታል።

የፍርስራሽ ክምር

“የፍርስራሽ ቁልል”

ፈጽሞ ዳግመኛ አትሠራ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከተማይቱን ማንም ደግሞ አይሥራት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 13:17

ለመጥፋት ከተለዩ ከእነዚያ ነገሮች አንዱም እጅህ ላይ አይጣበቅ

እግዚአብሔር አንድን ነገር መርገሙና ሊያጠፋው መማሉ እርሱ ቁሱን ከሌሎች ነገሮች ለይቶ እንደሚያስቀምጠው ሆኖ ተነግሯል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር አጥፋው ብሎ ካዘዘህ ነገር ውስጥ የትኛውንም ማቆየት የለብህም” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እጅህ ላይ አይጣበቅ

ይህ አንድ ሰው የሆነ ነገርን ለራሱ የሚያቆይበት መንገድ ነው። አ.ት፡ “አታቆይ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር ከቁጣው መዓት ይመለሳል

እግዚአብሔር ከእንግዲህ ያለመቆጣቱ ቁጣው እንደ አንድ ቁስ ተቆጥሮ እግዚአብሔር በአካል ከእርሱ እንደሚመለስ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር መቆጣቱን ይተዋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለአባቶችህ

እዚህ ጋ “አባቶችህ” ማለት አያቶችህ ወይም ቅድም አያቶችህ ማለት ነው።

የእግዚአብሔርን ድምፅ ሰምተሃል

እዚህ ጋ “ድምፅ” እግዚአብሔር የሚናገረውን ይወክላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የሚናገረውን ታዘሃል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በአምላክህ በእግዚአብሔር ዐይን ትክክል የሆነውን

ዐይን ማየትን ይወክላል፣ ማየትም ማሰብን ወይም መወሰንን ይወክላል። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ውሳኔ ትክክል የሆነውን” ወይም “አምላክህ እግዚአብሔር ትክክል እንደሆነ የሚቆጥረውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 14

1 እናንተ የእግዚአብሔር የአምላካችሁ ሕዝብ ናችሁ። ስለ ሞተው ሰው አካላችሁን አታቆስሉ፥ የትኛውንም የፊታችሁን ክፍል አትላጩ። 2 ምክንያቱም እናንተ ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ ቅዱስ ሕዝብ ናችሁ፤ በምድርም ላይ ከሚኖሩ አሕዛብ ሁሉ ይልቅ ለራሱ ሕዝብ ትሆኑ ዘንድ አምላካችሁ እግዚአብሔር እናንተን መርጦአልና። 3 ርኩስን ነገር ሁሉ አትብሉ። 4 የምትበሉአቸው እንስሶች እነዚህ ናቸው፦ በሬ፥ በግ፥ ፍየል፥ 5 ዋላ፥ ሚዳቋ፥ የበረሃ አጋዘን፥ አጭ፥ በራይሌ፥ የተራራ በግ (ድኩላ)። 6 ከእንስሶች ሰኮናው የተሰነጠቀውን ጥፍሩም ከሁለት የተከፈለውን የሚያመነዥከውንም እንስሳ ሁሉ ትበላላችሁ። 7 ነገር ግን ከማያመሰኩ ወይም ሰኮናቸው ካልተሰነጠቀ፥ እነዚህን አትበሉም፤ ግመል፥ ጥንቸል፥ ሽኮኮን፥ አትበሉም። የሚያመነዥኩና ነገር ግን ሰኮናቸው ያልተሰነጠቀም እነዚህ ለእናንተ ርኩሶች ናቸው። 8 እርያም ሰኮናው ስለ ተሰነጠቀ ነገር ግን ስለማያመነዥክ፥ እርሱ ለእናንተ ርኩስ ነው፤ ሥጋውን አትብሉ በድኑንም አትንኩ። 9 በውኃ ውስጥ ከሚኖሩት ሁሉ የምትበሉአቸው እነዚህ ናቸው፤ ክንፍና ቅርፊት ያላቸውን ትበላላችሁ። 10 ነገር ግን ክንፍና ቅርፊትም የሌላቸውን አትበሉም፥ ለእናንተ ርኩስ ናቸው። 11 ንጹሕ የሆኑትን ወፎችን ሁሉ ትበላላችሁ። 12 ነገር ግን ከወፎች ሊበሉ የማይገባቸው እነዚህ ናቸው። ንስር፥ ገዴ፥ ዓሣ አውጭ፥ 13 ጭልፊት፥ ጭላት፥ በየወገኑ፥ 14 ቁራም ሁሉ በየወገኑ፥ 15 ሰጎን፥ ጠላቋ፥ ዝዪ፥ በቃል፥ በየወገኑ፥ 16 ጉጉት፥ ጋጋኖ፥ 17 የውኃ ዶሮ ይብራ፥ 18 ጥምብ አንሣ፥ አሞራ፥ እርኩም ሽመላ ሳቢሳ፥ በየወገኑ፥ ጅንጅላቴ ወፍ፥ የሌሊት ወፍ፥። 19 የሚበርርም ተንቀሳቃሽ ሁሉ ለእናንተ ርኩስ ነው፤ አይበሉም። 20 ንጹሕ የሆኑትን ወፎች ሁሉ ብሉ። 21 የበከተውን ሁሉ አትብሉ፥ ይበላው ዘንድ በአገራችሁ ደጅ ለተቀመጠ፥ መጻተኛ ትሰጠዋላችሁ፥ ወይም ለእንግዳ ትሸጣላችሁ። ምክንያቱም እናንተ ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ የተቀደሰ ሕዝብ ናችሁ። የፍየሉን፥ ጠቦት፥ በእናቱ ወተት አትቀቅሉ። 22 ከእርሻችሁ በየዓመቱ ከምታገኙት ከዘራችሁ ፍሬ ሁሉ አሥራት ታወጣላችሁ። 23 ሁልጊዜ እግዚአብሔር አምላካችሁን መፍራት ትማሩ ዘንድ ስሙ፤ እንዲጠራበት በመረጠው ስፍራ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት የእህላችሁን የወይን ጠጃችሁንም የዘይታችሁንም አሥራት የላማችሁንና የበጋችሁንም በኩራት ብሉ። 24 እግዚአብሔር አምላካችሁ በባረካችሁ ጊዜ መንገዱ ሩቅ ቢሆን፥ እግዚአብሔር አምላካችሁም ስሙን ያኖርበት ዘንድ የመረጠው ስፍራ ቢርቅባችሁ ግን ወደዚያ ለመሸከም ባትችሉ ትሸጣላችሁ፥ 25 የዋጋውንም ገንዘቡ በእጃችሁ ይዛችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ ወደ መረጠው ስፍራ ትሄዳላችሁ። 26 በዚያም በገንዘቡ የፈለጋችሁትን በሬ ወይም፥ በግ ወይም፥ የወይን ጠጅ፥ ወይም ብርቱ መጠጥ፥ ወይም የፈለጋችሁትን ሁሉ ትገዛላችሁ፤ በዚያም በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ትበላላችሁ፥ እናንተና ቤተ ሰባችሁም ደስ ይላችኋል። 27 ድርሻና ርስት ከእናንተ ጋር ስለሌለው በአገራችሁ ደጅ ውስጥ ያለውን ሌዋዊውን ቸል አትበሉ። 28 በየሦስተኛው ዓመት መጨረሻ በዚያ ዓመት ሌዋዊው ከእናንተ ጋር ክፍልና ርስት ስለሌለ የፍሬአችሁን አሥራት ሁሉ አምጥታችሁ በአገራችሁ ደጅ ታኖራላችሁ፤ 29 በአገራችሁም ደጅ ያለ መጻተኛ፥ ድሀ አደግ፥ ባል የሞተባት መጥተው ይበላሉ፤ ይጠግባሉም። ይኸውም እግዚአብሔር አምላካችሁ በምታደርጉት በእጃችሁ ሥራ ሁሉ ይባርካችሁ ዘንድ ነው።



Deuteronomy 14:1

እናንተ -- ሕዝብ ናችሁ -- እናንተ -- የተለየ ሕዝብ ናችሁ -- መርጧችኋል

“እናንተ” የሚለው አገባብ በሙሉ የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። ሙሴ የሕዝቡ አካል ሆኖ ተካቶአል። አ.ት፡ “እኛ… ሕዝብ ነን … እኛ የተለየን ሕዝብ ነን … መርጦናል”

ስለሞተው ራሳችሁን አትቁረጡ ወይም ከፊታችሁ የትኛውንም ክፍል አትላጩት

እነዚህ በከነዓን ይኖሩ የነበሩት የሕዝብ ወገኖች ለሞቱ ሰዎች ሐዘናቸውን የሚገልጹበት መንገድ ነበር። ሙሴ እንደዚያ እንዳያደርጉ ለእስራኤል ሕዝብ ይነግራቸዋል። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። (See: Symbolic Action and Assumed Knowledge and Implicit Information)

ከፊታችሁ የትኛውንም ክፍል አትላጩት

“ከራሳችሁ ጸጉር ላይ ከፊት ያለውን አትላጩት”

በምድር ፊት -- እናንተ የተለየ ሕዝብ ናችሁ

እነዚህን ቃላት በዘዳግም 7፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር የተለየ ሕዝብ ናችሁ

እግዚአብሔር በልዩ ሁኔታ የእርሱ እንዲሆኑ የእስራኤልን ሕዝብ መምረጡ እነርሱን ከሌሎች ሕዝቦች ሁሉ እንደለያቸው ተደርጎ ተነግሯል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አምላካችሁ እግዚአብሔር እናንተን ከሌሎች ሕዝቦች ለይቶአችኋል” (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት))

እግዚአብሔር የራሱ ንብረት የሆነ ሕዝብ እንድትሆኑ መርጧችኋል

ይህ ማለት በመሠረቱ ከዐረፍተ ነገሩ መጀመሪያ ጋር ተመሳሳይ ነገር ነው። ሁለቱም የሚሉት የእስራኤል ሕዝብ በልዩ ሁኔታ የእግዚአብሔር መሆኑን ነው። (See: Parallelism)

የራሱ ንብረት የሆነ ሕዝብ

“የግል ንብረቱ የሆነ ሕዝብ” ወይም “የእርሱ ሕዝብ”

በምድር ፊት ከሚኖሩ ሕዝቦች ሁሉ በላይ

“በዐለም ላይ ካሉ የሕዝብ ወገኖች ሁሉ”

Deuteronomy 14:3

የትኛውንም ንጹሕ ያልሆነ ነገር አትብላ

የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሔር መበላት የለባቸውም ያላቸውን የትኛውንም ነገር መብላት አይጠበቅባቸውም።

አጋዘን፣ ሚዳቋ፣ ሰስ

እነዚህ የተለያዩ ዓይነት አጋዘኖች ናቸው። የአንተ ቋንቋ እያንዳንዱን እንስሳ የሚወክል ቃል ከሌለው “ልዩ ልዩ ዓይነት አጋዘን” ተብሎ ሊተረጎም ይችላል።

ሚዳቋ

ይህ በፍጥነት መሮጥ የሚችል ቀጭንና ረጅም እግር ያለው የዱር እንስሳ ነው። ይህንን በዘዳግም 12፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሰስ

የአጋዘን ዓይነት (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

ዋሊያ እና ድኩላ

እነዚህ ሁለቱም የድኩላ ዓይነቶች ናቸው። የአንተ ቋንቋ እያንዳንዱን እንስሳ የሚወክል ቃል ከሌለው “የተለያዩ የድኩላ ዓይነቶች” ተብሎ ሊተረጎም ይችላል።

ዋሊያ

የድኩላ ዓይነት (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:6

ሰኮናው የተከፈል

“የተሰነጠቀ ሰኮና ያለው”። ይህ ሰኮናው አንድ ሙሉ ከመሆን ይልቅ ሁለት ቦታ የተሰነጠቀ ነው።

የሚያመነዥክ

ይህ ማለት እንስሳው ምግቡን ከሆዱ ውስጥ እያመጣ እንደገና ያኝከዋል።

ጥንቸል

ይህ ረጃጅም ጆሮዎች ያሉት ትንሽ እንስሳ ሲሆን አብዛኛውን ጊዜ የሚኖረው ምድር ላይ በጉድጓዶች ውስጥ ነው። (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

ሽኮኮ

ይህ ትንሽ እንስሳ ሲሆን የሚኖረው በዐለታማ አካባቢ ነው። (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

እነርሱ ለእናንተ ንጹሕ አይደሉም

እግዚአብሔር ሕዝቡ ሊበላው አይገባውም የሚለው አንዳች ነገር በአካላዊነቱም ንጹሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:8

ዐሳማ ለእናንተ ንጹሕ አይደለም

እግዚአብሔር ሕዝቡ ሊበላው አይገባውም የሚለው አንዳች ነገር በአካላዊነቱም ንጹሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:9

በውሃ ውስጥ ከሚኖሩት እነዚህን መብላት ትችላላችሁ

“በውሃ ውስጥ ከሚኖሩት እነዚህን የመሳሰሉትን እንስሳት መብላት ትችላላችሁ”

ግልፋፊ

ዓሳ በውሃ ውስጥ ለመንቀሳቀስ የሚጠቀምበት ቀጭንና ሰፋ የሚል የአካል ክፍሉ

ቅርፊት

የዓሳውን አካል የሚሸፍኑ ትናንሽ ንብርብሮች

ለእናንተ ንጹሐን አይደሉም

እግዚአብሔር ሕዝቡ ሊበላው አይገባውም የሚለው አንዳች ነገር በአካላዊነቱም ንጹሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:11

ንጹሕ የሆነ ወፍ ሁሉ

እግዚአብሔር ሕዝቡ ሊበላው ይችላል የሚለው እንስሳ፣ ያ እንስሳ በአካላዊነቱም ንጹሕ እንደሆነ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ንስር - ጥምብ አንሣ - ዓሳ አውጪ - ቀይ ጭልፊት - ጥቁር ጭልፊት - ገዴ

እነዚህ በሌሊት የሚንቀሳቀሱ ወይም ትናንሽ እንስሳትንና የሞቱ እንስሳትን የሚመገቡ የወፍ ዝርያዎች ናቸው። (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:14

ቁራ - የባህር ወፍ

እነዚህ በሌሊት የሚንቀሳቀሱ ወይም ትናንሽ እንስሳትንና የሞቱ እንስሳትን የሚመገቡ ሁሉም ዓይነት ወፎች ናቸው። (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:18

ሽመላ - የውሃ ወፍ፣ እርኩም

እነዚህ ትናንሽ እንስሶችንና እንሽላሊቶችን የሚመገቡ የወፍ ዓይነቶች ናቸው። (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

የሌሊት ወፍ

በተለይ በምሽት የሚበር፣ ነፍሳትንና ዐይጦችን የሚመገብ፣ ክንፍና ጸጉራማ አካል ያለው እንስሳ

ክንፍ ያላቸው ጥቃቅን ነፍሳት ሁሉ

ይህ ማለት በመንጋ ሆነው የሚንቀሳቀሱ በራሪ ነፍሳት ሁሉ ማለት ነው።

ለእናንተ ንጹሕ አይደሉም

እግዚአብሔር ሕዝቡ ሊበላው አይገባውም የሚለው እንስሳ በአካላዊነቱም ንጹሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መበላት የለባቸውም

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ልትበሏቸው አይገባም” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕ ሆነው የሚበሩ ነገሮች

እግዚአብሔር ሕዝቡ ሊበላው ይችላል የሚለው እንስሳ፣ ያ እንስሳ በአካላዊነቱም ንጹሕ እንደሆነ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:21

የትኛውንም የሞተ ነገር አትብላ

ይህ በተፈጥሮአዊ ሞት የሚሞተውን እንስሳ ማለት ነው።

እንተ ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር የተለየ ሕዝብ ናችሁና

እግዚአብሔር በልዩ ሁኔታ የእርሱ እንዲሆኑ የእስራኤልን ሕዝብ መምረጡ እነርሱን ከሌሎች ሕዝቦች ሁሉ እንደለያቸው ተደርጎ ተነግሯል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አምላካችሁ እግዚአብሔር እናንተን ከሌሎች ሕዝቦች ለይቶአችኋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:22

ከእርሻህ ከምታገኘው ምርት ሁሉ

ይህ ከምርታቸው ከየአሥሩ እጅ አንድ እጁን እንዲሰጡ ማለት ነው።

በዓመት በዓመቱ

“በየዓመቱ”

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ሀልዎት ፊት”

Deuteronomy 14:24

እርሱን ይዘህ

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚያመለክተው የምርቱንና የቀንድ ከብቱን አስራት ነው።

መባውን ወደ ገንዘብ ቀይረው

“መባህን በገንዘብ ትሸጠዋለህ”

ገንዘቡን በእጅህ ይዘህ ሂድ

“ገንዘቡን በቦርሳ አድርገህ ይዘኸው ሂድ”

Deuteronomy 14:26

ያሻህን ሁሉ

“የምትፈልገውን ሁሉ”

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ሀልዎት ፊት”

በበርህ ውስጥ ያለ ሌዋዊ

እዚህ ጋ “በር” የሚወክለው ከተማውን ወይም መንደሩን በሙሉ ነው። አ.ት፡ “በከተማህ ውስጥ የሚኖረውን ሌዋዊ ሁሉ” (See: Synecdoche)

አትርሳው

ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከአስራትህ ጥቂቱን ለሌዋዊው ስለመስጠትህ እርግጠኛ” (See: Double Negatives)

ከአንተ ጋር ድርሻም ሆነ ርስት የለውምና

የሌዊ ነገድ ርስት የሚሆናቸውን የመሬት ድርሻ አልወሰዱም። የእግዚአብሔር ካህናት ሆነው እርሱ ማገልገላቸው የእነርሱ የርስት ድርሻ ነው። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ድርሻም ሆነ ርስት የለውም

እግዚአብሔር ለሌዋውያን መሬት አለመስጠቱ ርስት እንዳልሰጣቸው ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 14:28

በየሦስተኛው ዓመት ከምርትህ ሁሉ አስራት አቅርብ

ለሌዋውያን፣ ወላጆቻቸውን ላጡ ልጆች፣ ለመበለቶችና መጻተኞች እንዲሰጣቸው እስራኤላውያን በ3 ዓመት አንድ ጊዜ አስራታቸውን በየከተማቸው ማከማቸት ነበረባቸው። (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በበሮችህ ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክሉት ከተማውን ወይም መንደሩን በሙሉ ነው። አ.ት፡ “በከተማህ ውስጥ” (See: Synecdoche)

ከአንተ ጋር ድርሻም ሆነ ርስት የለውምና

እግዚአብሔር ለሌዋውያን ምንም መሬት አለመስጠቱ ርስት እንዳልሰጣቸው ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወላጆቻቸውን ያጡ

እነዚህ ሁለቱም ወላጆቻቸው የሞቱባቸውና የሚንከባከባቸው ዘመድ የሌላቸው ልጆች ናቸው።

መበለት

ይህቺ ባል የሞተባትና በእርጅናዋ የሚረዳት ልጅ የሌላት ሴት ናት።

በምትሠራው የእጅህ ሥራ ሁሉ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው የሰውን ሁለንተናውን ነው። ይህ የሚያመለክተው አንድ ሰው የሚሠራውን ሥራ ነው። አ.ት፡ “በምትሠራው ሥራ ሁሉ” (See: Synecdoche)


Chapter 15

1 በየሰባት ዓመት የዕዳ ምሕረት ታደጋላችሁ። 2 ይህ ዕዳ ምሕረት አፈጻጸም እንከሚከተለው ነው፤ አበዳሪ ሁሉ ለባልንጀራው ላበደረው እንዲተውዋውና ከባልጀራው ወይም ወንድሙ መልሶ እንዳይጠይቅ እግዚአብሔር ያወጀው ይህ ነው። 3 ለእንግዳ ያበደራችሁትን መጠየቅ የምትችሉ ሲሆን፥ ለእስራኤላዊ ወንድማችሁ ያበደራችሁትን ግን ምሕረት አድርጉለት። 4 ይሁን እንጂ፥ አምላካችሁ እግዚአብሔር ትወርሱአት ዘንድ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ ምድር ውስጥ አብዝቶ ስለሚባርካችሁ በመካከላችሁድኻ አይኖርም። 5 ይህ የሚሆነው የእግዚአብሔር የአምላካችሁን ድምፅ ፈጽማችሁ ስትሰሙና ዛሬ የማዛችሁን ትእዛዘትን ሁሉ ስትታዘዙ ብቻ ነው። 6 እግዚአብሔር አምላካችሁ በሚሰጣችሁ ተሰፋ መሠረት ስለሚባርካችሁ እናንተ ለብዙ አሕዛብ ታበድራላችሁ እንጂ እናንተ አትበደሩም፤ብዙ አሕዛብን ትገዛላችሁ እንጂ ማንም እናንተን አይገዛችሁም። 7 እግዚአብሔር አምላካችሁ በሚሰጣችሁ ምድር ላይ ደኻ ቢኖር፥ በደኻ ወንድማችሁ ላይ ልባችሁ አይጨክን፥ለደኻ ወንድማችሁ ላይም እጃችሁን ከመዘርጋት አትቆጥቡ፤ 8 ነገር ግን እጃችሁን በትክክል ፍቱለት ለማያስፈልገውም ቅር ሳትሉ አበድሩት። 9 ዕዳ የሚሠርዝበት ሰባተኛ ዓመት ቀርቦአል፥ በማለት ክፉ አሳብ አድሮባችሁ በችግረኛ ወንድማችሁ ላይ እንዳትጨክኑና ምንም ሳትሰጡት እንዳይቀር እርሱ በእናንተ ላይ ወደ እግዚአብሔር ጮኾ በደለኞች እንዳትሆኑ ተጠንቀቁ። 10 በቅን ልቦና ስጡት፥ ስትሰጡትም ልባችሁ አይጸጸት፥ከዚያም የተነሣ ግዚአብሔር አምላካችሁ ሥራችሁንና እጃችሁን ያረፈበትን ሁሉ ይባርክላችኋል። 11 በምድሪቱ ላይ ሁልጊዜ ድኾች አይጠፉም፥ስለዚህ በዚያ ለሚኖሩ ወንድሞቻችሁ ለድኾችና ለችግራኞች እጃችሁን እንድትዘረጉ አዛችኋለሁ። 12 እናንተም ወንድማችሁን ዕብራዊውን ወይም ዕብራዊቱን ብትገዙ ስድስት ዓመት ያገልግላችሁ በሰባተኛውም ዓመት ከእናንተ ዘንድ አርነት አውጡት። 13 ከእናንተም ዘንድ አርነት በሚታወጣበት ጊዜ ባዶውን አትስደዱት። 14 ነገር ግን ከመንጋህ፥ ከአውድማችሁም፥ ከወይራችሁም መጥመቂያም ትለግሱታላችሁ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ በባረካችሁ መጠን ትሰጡት ዘንድ ይገባል። 15 እናንተም በግብፅ አገር ባሮች እንደ ነበራችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁም እንደ ነበራችሁ አስቡ፤ስለዚህ እኔ ዛሬ ይህን እንድታደርጉ አዛችሁኋለሁ። 16 ነገር ግን አገልጋያችሁ እናንተንና ቤተ ሰቦቻችሁን በመውደዱና ከእናንተ ጋር ደስተኛ ሆኖ ከመኖሩ የተነሣ፦ ከእናንተ መለየት አልፈልግም ቢላችሁ፦ 17 ጆሮውን ከቤታችሁ መዝጊያ ላይ በማስደግፍ በወስፌ ትበሳላችሁ፤ከዚያም ዕድሜ ልኩን አገልጋያችሁ ይሆናል። በቤት አገልጋዮችሁም ላይ እንዲሁ አድርግ። 18 አገልጋያችሁን አርነት ማውጣት ከባድ መስሎ አይታያችሁ፤ ምክንያቱም የስድስት ዓመት አገልግሎቱ አንድ የቅጥር ሠራተኛ ከሚሰጠው አገልግሎት እጥፍ ነውና። እግዚአብሔር አምላካችሁ በምታደጉት ነገር ሁሉ ይባርካችኋልና። 19 የቀንድ ከብት፥ የበግና የፍየል መንጋዎቻችሁን ተባዕት በኩር ሁሉ ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ ቀድሱ። የበሬአችሁን በኩር አትሥሩባቸው፥ የበጋችሁንም በኩር አትሸልቱ፥ 20 እርሱ በሚመርጠው ስፍራ እናንተና ቤተ ሰባችሁ በየዓመቱ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ትበሉታላችሁ። 21 አንድ እንስሳ እንከን ካለበት፤ አንካሳ ወይም ዕውር ወይም ደግሞ ማናቸውም ዓይነት ከባድ ጉድለት ያለበት ከሆነ፤ ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር አትሠዉ። 22 የከተሞቻችሁ ትበላላችሁ፤ በሥርዓቱ መሠረት ንጹሕ የሆነውም ሆነ ያልሆነው ሰው፥ እንደ ድኩላ እንደ ዋላ ያሉትን ይበላዋል። 23 ደሙን እንደ ውሃ መሬት ላይ አፍስሱት እንጂ አትብሉት።



Deuteronomy 15:1

ሰባት ዓመት

“7 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ዕዳ ሰርዝ

“ሰዎች የተበደሩህን ሁሉ ተውላቸው”

ምሕረት የምታደርገው እንደዚህ ነው

“ዕዳውን የምትሰርዘው እንደዚህ ነው”

አበዳሪ

ለሌሎች ሰዎች ገንዘብ የሚያበድር ሰው

ጓደኛውን ወይም ወንድሙን

“ጓደኛ” እና “ወንድም” የሚሉት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም የሚጋሩ ሲሆኑ ከሌላው እስራኤላዊ ወዳጃቸው ጋር ባላቸው የቅርብ ግንኙነት ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “እስራኤላዊ ጓደኛው” (See: Doublet)

እግዚአብሔር የዕዳ ምሕረት ዐውጆአልና

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ዕዳን እንድትምር እግዚአብሔር አዞሃልና” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እጅህ መተው አለበት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንዲመለስልህ መጠየቅ የለብህም” ወይም “ተመልሶ እንዲከፈልህ መጠየቅ የለብህም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 15:4

ድኻ አይኖርም

“ድኻ” የሚለው ስማዊ ቅጽል እንደ ቅጽል ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ድኻ ሕዝብ” ውይም “ድኻ የሚሆን አንድም ሰው” (See: Nominal Adjectives)

የሚሰጣችሁ ምድር

ይህ የከነዓንን ምድር ያመለክታል።

እንድትወርሰው ርስት አድርጎ በሚሰጥህ

እግዚአብሔር ለሕዝቡ የሚሰጣቸው ምድር ርስታቸው እንደሚሆን ተቆጥሮ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የአምላክህን የእግዚአብሔርን ድምፅ በጥንቃቄ የምትሰማ ከሆነ ብቻ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው ራሱን እግዚአብሔርን ነው። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር የሚናገረውን ለመታዘዝ ከተጠነቀቅህ ብቻ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ታበድራለህ -- አትበደርም

“ገንዘብ” የሚለው ቃል የሚታወቅ ነው። የዚህን መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “ገንዘብ ታበድራለህ … ገንዘብ አትበደርም” (See: Ellipsis)

ለብዙ ሕዝቦች -- በብዙ ሕዝቦች ላይ

እዚህ ጋ “ሕዝቦች” የሚወክሉት ሰዎችን ነው። አ.ት፡ “ለብዙ ሀገር ሰዎች … በብዙ ሀገር ሰዎች ላይ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በብዙ ሕዝቦች ላይ ትገዛለህ፣ እነርሱ ግን በአንተ ላይ አይገዙም

እዚህ ጋ “መግዛት” በገንዘብ ዐቅም መብለጥ ማለት ነው። ይህ ትርጉሙ በዐረፍተ ነገሩ የመጀመሪያ ክፍል ካለው ጋር ተመሳሳይ ነው። (See: Parallelism)

Deuteronomy 15:7

ድኻ የሆነ ሰው ቢኖር

እዚህ ጋ “ሰው” ማለት በጥቅሉ ሰው ነው። አ.ት፡ “ድኻ የሆነ ሰው ቢኖር”

ከውንድሞችህ አንዱ

“ከእስራኤላዊ ጓደኞችህ አንዱ”

ከበሮችህ በአንዱ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክሉት ከተማን ወይም መንደርን በሙሉ ነው። አ.ት፡ “በየትኛውም ከተማህ” (See: Synecdoche)

ልብህን አታደንድን

ግትር መሆን ሰዎቹ ልባቸውን እንዳደነደኑ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ግትር አትሁን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከድኻው ወንድምህ እጅህን አትክደን

ለድኻው ሰው ለመስጠት የማይፈቅድ ሰው ድኻው ሰው ከእርሱ ምንም እንዳያገኝ እጁን እንደሚከድን ተደርጎ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “ድኻ የሆነውን እስራኤላዊ ጓደኛህን ለመርዳት እምቢ አትበል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ነገር ግን እጅህን ልትዘረጋለት በእርግጥ ይገባል

ድኻውን ሰው የሚረዳ እጁን እንደ ከፈተለት ተደርጎ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “ነገር ግን ልትረዳው በእርግጥ ይገባሃል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 15:9

የሚል ክፉ አሳብ በልብህ አይኑር

እዚህ ጋ “ልብ” የሚወክለው የሰውን አዕምሮ ነው። አ.ት፡ “ክፍ አሳብ አታስብ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰባተኛው ዓመት፣ የምሕረት ዓመት ቀርቧል

ይህ የምሕረት ዓመት ስለቀረበ ይህንን የሚያስበው ሰው ድኻው ሰው ሊመልስለት እንደማይችል በማሰብ ድኻውን ለመርዳት እንደሚያመነታ ያመለክታል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ሰባተኛው ዓመት

“ሰባተኛው” የሚለው ቃል የሰባት ደረጃ አመልካች ቁጥር ነው። (ደረጃን አመልካች ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

የምሕረት ዓመት

“ዕዳን የመሰረዝ ዓመት”

ቀርቧል

በቅርብ የሚሆን አንድ ነገር በአካል የቀረበ በሚመስል መልኩ ተነግሯል። አ.ት፡ “በቅርቡ ይሆናል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስስታም ሆነህ ለድኻው ወንድምህ ሳትሰጠው እንዳትቀር

“አትጨክን፣ ለእስራኤላዊ ጓደኛህ የትኛውንም ነገር ከመስጠት አትንፈገው”

ወደ እግዚአብሔር ያለቅሳል

“ዕርዳታ ለማግኘት ወደ እግዚአብሔር ይጮኻል”

ኃጢአት ይሆንብሃል

“አንተ ያደረግኸውን እግዚአብሔር ኃጢአት ይለዋል”

ልብህን አይጸጽተው

እዚህ ጋ “ልብ” ሙሉውን ሰው ይወክላል። አ.ት፡ “ቅር አይበልህ” ወይም “ደስ ይበልህ” (Synecdoche እና ምጸት የሚለውን ተመልከት)

እጅህን በምታኖርበት ሁሉ

እዚህ ጋ “እጅህን በምታኖርበት” የሚወክለው ሙሉውን ሰውና እርሱ የሚሠራውን ሥራ ነው። አ.ት፡ “በምትሠራው ሁሉ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 15:11

ድኻ ከምድር ላይ አይጠፋምና

ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በምድር ላይ ድኾች ሁሌም ይኖራሉና” (ድርብ አሉታ የሚለውን ተመልከት)

ድኾች

“ድኾች” የሚለው ስማዊ ቅጽል እንደ ቅጽል ሆኖ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ድኾች ሰዎች” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

‘በምድርህ ላይ -- እጅህን መክፈት አለብህ’ ብዬ አዝሃለሁ

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ ነው። ቀጥተኛው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ተደርጎ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በምድርህ ላይ -- እጅህን እንድትከፍት አዝሃለሁ” (በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ እና ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ)

ለወንድምህ፣ ለችግረኛና ለድኻው እጅህን ክፍት

አንድን ሰው ለመርዳት ፈቃደኛ የሚሆን ሰው እጁን እንደሚከፍት ተደርጎ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “እስራኤላዊ ጓደኛህን፣ የተቸገሩትንና ድኾችን እርዳቸው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለወንድምህ፣ ለችግረኛና ለድኻው

“ችግረኛ” እና “ድኻ” የሚሉት ቃላት መሠረታዊ ትርጉማቸው አንድ ሆኖ እነዚህ ራሳቸውን መርዳት የማችሉ ሰዎች መሆናቸው ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “ራሳቸውን መርዳት የማይችሉ እስራኤላውያን ጓደኞችህን እርዳቸው” (See: Doublet)

Deuteronomy 15:12

ወንድምህ

እዚህ ጋ “ወንድም” ማለት ወንድ ይሁን ሴት በአጠቃላይ እስራኤላዊ የሆነ ማለት ነው። አ.ት፡ “አንድ እስራኤላዊ ጓደኛህ” ወይም “አንድ ዕብራዊ ጓደኛህ” (ተባዕታዊ ቃል ሴቶችን ሲጨምር የሚለውን ቃል ተመልከት)

ለአንተ የተሸጠ

አንድ ሰው ዕዳውን መክፈል ባይችል አንዳንድ ጊዜ የተበደረውን ለመክፈል ራሱን ለባርነት ይሸጥ ነበር። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ራሳቸውን ለአንተ የሸጡ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ስድስት ዓመት

“6 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሰባተኛ ቁጥር

“7 ዓመት”። ይህ “ሰባተኛ” የሰባት ደረጃን አመልካች ቁጥር ነው። (ደረጃን አመልካች ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

ባዶ እጁን እንዲሄድ አታድርግ

ለራሱ ወይም ለቤተሰቡ የሚያቀርበው አስፈላጊ ነገር የሌለው ሰው እጆቹ ባዶ እንደሆኑ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ለእርሱና ለቤተሰቡ የሚያቀርበው እንዲኖረው ሳትሰጠው እንዲሄድ አታድርገው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በልግስና ስጠው

“በደግነት ስጠው”

Deuteronomy 15:15

ባሪያ እንደነበርህ አስብ

እዚህ ጋ “አንተ” የሚለው ቃል ለብዙ ዓመታትባሪያዎች የነበሩትን ቅድም አያቶቹን ይጨምራል። አ.ት፡ “በአንድ ወቅት የአንተም ሕዝብ ባሪያዎች እንደነበሩ አስብ” (See: Forms of You)

አምላክህ እግዚአብሔር ተቤዥቶሃል

እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ በግብፅ ባሪያ ከነበረበት ማዳኑ ሕዝቡን ከባርነት ለመቤዠት ገንዘብ የከፈለ በሚመስል መልኩ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

‘ከአንተ አልለይም’ ቢልህ

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ ነው። ቀጥተኛ የሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከአንተ አልለይም ቢልህ” (በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ እና ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ

ቤትህ

እዚህ ጋ “ቤት” የሚወክለው የሰውየውን ቤተሰብ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም ወስፌ ወስደህ በሩ ላይ አስደግፈህ ጆሮውን ትበሳዋለህ

“ከዚያም ራሱን በቤትህ የበር መቃን ላይ ታስደግፍና በጆሮው የጉትቻ ማንጠልጠያ ቦታ ላይ የወስፌው ጫፍ እንጨቱ ጋ እስኪደርስ ትበሳዋለህ”

ወስፌ

ቀዳዳ ለማበጀት የሚጠቅም ጫፉ የሾለና ቀጥ ያለ መሣሪያ (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

ዕድሜ ልኩን

“እስከ ሕይወቱ መጨረሻ ድረስ” ወይም “እስኪሞት ድረስ”

Deuteronomy 15:18

በነጻ ማሰናበቱ አስቸጋሪ ሆኖ አይሰማህ

ይህ ማለት አንድን ሰው በነጻ በሚያሰናብቱበት ጊዜ ቅር መሰኘት የለባቸውም። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በነጻ በምታሰናብተው ጊዜ ደስ ይበልህ” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

የቅጥር ሠራተኛውን ዕጥፍ ዋጋ ተቀብለሃል

ይህ ማለት ባለቤቱ ሥራ ለማሠራት ከሚቀጥረው ሰው ባነሰ ዋጋ ብቻ ይህንን ባሪያ አሠርቶታል ማለት ነው።

የተቀጠረ ሰው

ይህ ተከፍሎት የሚሠራ ሰው ማለት ነው።

Deuteronomy 15:19

መሸለት

ሱፍ ወይም ጸጉር መቁረጥ

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ሀልዎት ፊት”

ዓመት በዓመት

“በእያንዳንዱ ዓመት” ወይም “በየዓመቱ”

አንካሳ

ሽባ ወይም አካሉ የተጎዳ

Deuteronomy 15:22

በበሮችህ ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክሉት ከተማውን ወይም መንደሩን ነው። አ.ት፡ “በማኅበረሰብህ ውስጥ” ወይም “በከተማህ ውስጥ” (See: Synecdoche)

ንጹሕ ያልሆኑ -- ሰዎች

ለእግዚአብሔር አገልግሎት ተቀባይነት የሌለው ሰው በአካሉም ንጹሕ እንዳልሆነ ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ንጹህ የሆኑ ሰዎች

ለእግዚአብሔር አገልግሎት ተቀባይነት ያለው ሰው በአካሉም ንጹሕ እንደሆነ ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሚዳቋ ወይም ድኩላ

እነዚህ በፍጥነት መሮጥ የሚያስችል ረጅምና ቀጭን እግሮች ያሏቸው የዱር እንስሳት ናቸው። እነዚህን በዘዳግም 12፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ደሙን አትብላ

“ደሙን አትመገበው”። ደም ሕይወትን ስለወከለ እስራኤላውያን ደም እንዲመገቡ እግዚአብሔር አልፈቀደላቸውም። (ዘዳግም 12:23ን ተመልከት)


Chapter 16

1 እግዚአብሔር አምላካችሁ በአቢብ ወር ከግብፅ በሌሊት ስላወጣችሁ የአቢብ ወር ጠብቁ፥ የእግዚአብሔር የአምላካችሁን ፋሲካ አክብሩበት። 2 እግዚአብሔር ለሰሙ ማደሪያ ይሆን ዘንድ በሚመርጠው ስፍራ ከበግና ከፍየል ወይም ከመንጋችሁ አንዱን እንስሳ እግዚአብሔር በአምላካችሁ ፋሲካ አድርጋችሁ ሠዉ። 3 ከቦካ ቂጣ ጋር አትብሉ፤ ከግብፅ የወጣችሁ በችኮላ ነውና፥ ከግብፅ የወጣችሁበትን ጊዜ በሕይወታችሁ ዘመን ሁሉ ታስቡ ዘንድ ያልቦካ ቂጣ ሰባት ቀን ብሉ። 4 ከምድራችሁ ሁሉ ላይ በእናንተ ዘንድ ለሰባት ቀን እርሾ አይገኝ በመጀመሪያው ዕለት ምሽት ከምትሠዉም ላይ ማናቸውም ሥጋ እስከ ጧት ድረስ እንዲቆዩ አታድርጉ። 5 እግዚአብሔር አምላካችሁ በሚሰጣችሁ በማናቸውም ከተማ በሮች ላይ ፋሲካን መሠዋት አይገባችሁም። 6 በዚህ ፈንታ፥ ለስሙ ማደሪያ ይሆን ዘንድ እግዚአብሔር አምላካችን በመረጠው ስፍራ ፀሐይ ስትጠልቅ በምሽት ላይ ከግብፅ ከወጣችሁበት ሰዓት ላይ በዚያ ፋሲካ ሰዉ። 7 ሥጋውንም ጠብሳችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ በሚመርጠው ስፍራ ብሉ፥ ሲነጋም ወደ ድንኳናችሁ ተመልሳችሁ ሂዱ። 8 ለስድስት ቀንም ያልቦካ ቂጣ ብሉ፤ በሰባተኛው ቀን በእግዚአብሔር በአምላካችሁ የተቀደሰ ጉባኤ አድርጉ፤ ሥራም አትሥሩበት። 9 እህላችሁን ማጨድ ከምትጀምሩበት ዕለት አንሥቶ ለራሰችሁም ሰባት ሳምንታትን ቁጠሩ። 10 ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር አምላካችሁ በባረካችሁ መጠን በፈቃዳችሁ የምታመጡትን ስጦታ በማቅረብ በመከሩ በዓል እግዚአብሔር አምላካችሁን አክብሩ። 11 እናንተ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁ ወንዶችና ሴቶች አጋልጋዮቻችሁ በከተሞቻችሁ ያለ ሌዋዊና መጻተኛ በመካከላችሁ የሚኖሩ አባት የሌላቸውና ባል የሞተባቸው እግዚአብሔር አምላካችሁ ለስሙ ማደሪያ እንዲሆን በሚመርጠው ስፍራ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ደስ ይበላችሁ። 12 እናንተም በግብፅ ባሪያዎች እንደ ነበራችሁ አስታውሱ፥ እነዚህንም ሥርዓቶች በጥንቃቄ ጠብቁ አድርጉም። 13 የእህላችሁን ምርት ከዐውድማችሁ ፤ ወይናችሁንም ከመጭመቂያችሁ ከሰበሰባችሁ በኋላ የዳስን በዓል ሰባት ቀን አክብሩ። 14 በበዓላችሁ እናንተና ወንድና ሴት ልጆቻችሁ፥ ወንድና ሴት አገልጋዮቻችሁ፥ በከተማው ያለ ሌዋዊ መጻተኛ፥ አባት አልባውና ባል የሞተባት ደስ ይበላችሁ። 15 እግዚአብሔር በመረጠው ስፍራ ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ በዓሉን ሰባት ቀን አክብሩ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ በእህል ምርታችሁና በእጆቻችሁ ሥራ ሁሉ ይበርካችኋል፤ ደስታችሁም ፍጹም ይሆናል። 16 ወንዶቻችሁ ሁሉ በዓመት ሦስት ጊዜ በቂጣ በዓል፥ በመከር በዓልና በዳስ በዓል ላይ እርሱ በሚመርጠው ስፍራ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ይቅረቡ፥ ማንም ሰው በእግዚአብሔር ፊት ባዶ እጁን አይቅረብ፥ 17 በዚህ ፈንታ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ በባረካችሁ መጠን እያንዳንዱ እንደ ችሎታው ይስጥ። 18 እግዝዚአብሔር አምላካችሁ በሚሰጣችሁ ከተማ ሁሉ ለየነገዶቻችሁ ዳኞችንና አለቆችን ሹሙ፥ እነርሱም ሕዝቡን በቅን ፍርድ ይዳኙ፥ 19 ፍርድ አታዛቡ፥ አድልዎ አታደርጉ፥ ጉቦም አትቀበሉ፥ ጉቦ የጠቢባንን ዐይን ያሳውራል፤ የጻድቃንንም ቃል ያጣምማልና። 20 በሕይወት እንድትኖሩና እግዚአብሔር አምላካችሁ የሚሰጣችሁን ምድር እንድትወርሱ ቅን ፍርድን ብቻ ተከተሉ። 21 ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ በምታደርጉት መሠዊያ አጠገብ የአሼራን ምስል የእንጨት ዐምድ አታቁሙ። 22 እግዚአብሔር አምላካችሁ የሚጠላውን ማምለኪያ ዐምድ ለእናንተ አታቁሙ።



Deuteronomy 16:1

የአቢብ ወር

ይህ በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር የመጀመሪያው ወር ነው። እርሱ እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ከግብፅ አውጥቶ ያመጣበትን ጊዜ ያስታውሳል። በምዕራባውያኑ አቆጣጠር በመጋቢት መጨረሻና በሚያዝያ መጀመሪያ አካባቢ ነው። (የዕብራውያን ወራት እና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ፋሲካን ጠብቀው

“ፋሲካን ጠብቀው” በዓሉን ማክበርና የፋሲካን ምግብ መብላት እንዳለባቸው ያመለክታል። አ.ት፡ “የፋሲካን ምግብ አክብር” ወይም “የፋሲካን ምግብ ብላ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Infor- mation)

ፋሲካን ትሠዋለህ

እዚህ ጋ “ፋሲካ” የሚወክለው ለፋሲካ በዓል የሚሠዋውን እንስሳ ነው። አ.ት፡ “ለፋሲካ መሥዋዕት ታቀርባለህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 16:3

ከእርሱ ጋር

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚያመለክተው የሚሠዉትንና የሚበሉትን እንስሳ ነው።

ሰባት ቀን

“7 ቀን” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የመከራን እንጀራ

ይህ እርሾ የሌለበት እንጀራ ስም ነበር። ሙሉ ትርጉሙ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ይህ እንጀራ በግብፅ በነበራችሁበት ጊዜ ምን ያህል እንደተሰቃያችሁ ያስታውሳችኋል” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

በጥድፊያ ከግብፅ ምድር የወጣችሁበትን

ሕዝቡ በፍጥነት ግብፅን ለቀው መውጣት ስለነበረባቸው እርሾ ጨምረውበት እንጀራ ለመጋገር በቂ ጊዜ አልነበራቸውም። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግለጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በችኮላ ከግብፅ በወጣችሁ ጊዜ እርሾ የገባበት እንጀራ ለማዘጋጀት ጊዜ አልነበራችሁም” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

በሕይወት ዘመናችሁ ሁሉ ይህንን አድርጉ

“በሕይወት እስካላችሁ ድረስ”

ልብ በሉ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አስታውሱ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በመካከላችሁ ምንም እርሾ አይታይ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በመካከላችሁ ምንም እርሾ አይኑራችሁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በግዛታችሁ ሁሉ

“በክልሎቻችሁ ሁሉ ውስጥ” ወይም “በምድራችሁ ሁሉ ላይ”

የመጀመሪያ ቀን

ይህ “የመጀመሪያ” አንድን የሚያመለክት የደረጃ አመልካች ቁጥር ነው። (ደረጃን አመልካች ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 16:5

ፋሲካን መሠዋት አይኖርብህም

እዚህ ጋ “ፋሲካ” የሚወክለው የሚሠዋውን እንስሳ ነው። አ.ት፡ “ለፋሲካ እንስሳውን መሠዋት አይኖርባችሁም” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በየትኛውም የከተማችሁ በሮች

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክሉት ከተሞቹን ወይም መንደሮችን ነው። አ.ት፡ “በየትኛውም መንደሮችህ ውስጥ” (See: Synecdoche)

ፀሐይ በምትወርድበት

“ፀሐይ ስትጠልቅ”

Deuteronomy 16:7

መጥበስ ይኖርብሃል

“ማብስል ይኖርብሃል”

ስድስት ቀን

“6 ቀን” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሰባት ቀን

“ሰባተኛ” የሰባት ደረጃን አመልካች ቁጥር ነው (ደረጃን አመልካች ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

የተለየ ጉባዔ

“ልዩ ስብሰባ”

Deuteronomy 16:9

ሰባት ሳምንት ቁጠር

“7 ሳምንት ቁጠር” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

እህል ማጨድ ከምትጀምርበት ጊዜ ጀምሮ

“ማጨድ ከምትጀምርበት” የሚለው ሐረግ መከር መሰብሰብ የሚጀመርበትን ጊዜ ማመላከቻ መንገድ ነው። አ.ት፡ “እህል መሰብሰብ ከምትጀምርበት ጊዜ ጀምሮ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ማጭድ

ሣር፣ ሰብል፣ እና ወይን ለመቁረጥ የሚያገለግል ቆልማማ ምላጭ ያለው መሣሪያ ነው። (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

በእጅህ በምትሰጠው የበጎ ፈቃድ ስጦታ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “የበጎ ፈቃድ ስጦታህን ትሰጣለህ” (See: Synecdoche)

አምላክህ እግዚአብሔር በባረከህ መጠን

“አምላክህ እግዚአብሔር እንደ ሰጠህ ምርት መጠን”። ይህ ማለት ሰዎቹ ምን ያህል መስጠት እንደሚኖርባቸው የሚወስኑት በዚያ ዓመት ባመረቱት ምርት መጠን ይሆናል።

Deuteronomy 16:11

ወንድ ልጅህ፣ ሴት ልጅህ፣ ወንድ ባሪያህ፣ ሴት ባሪያህ፣ ሌዋዊው

እነዚህ አንድን ተለይቶ የታወቀን ሰው አያመለክቱም። የሚያመለክተው እንዲህ ያሉትን ሰዎች በአጠቃላይ ነው። አ.ት፡ “ወንዶች ልጆቻችሁን፣ ሴቶች ልጆቻችሁን፣ ወንዶች ባሪያዎቻችሁን፣ ሴቶች ባሪያዎቻችሁን፣ የትኛውንም ሌዋዊ” (See: Generic Noun Phrases)

በከተማህ በሮች ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክሉት ከተሞችን ወይም መንደሮችን ነው። አ.ት፡ “በመንደሮችህ ውስጥ” (See: Synecdoche)

መጻተኛው፣ አባት የሌላቸውንና መበለቶችን

ይህ የሚያመለክተው እንዲህ ያሉትን የመሰሉ ሰዎችን በአጠቃላይ ነው። አ.ት፡ “መጻተኞችን ሁሉ፣ ወላጆቻቸውን ያጡትን፣ መበለቶችን” (See: Generic Noun Phrases)

አባት የሌላቸውን

እነዚህ አባትና እናት የሞቱባቸውና የሚንከባከባቸው ዘመድ የሌላቸው ልጆች ናቸው።

መበለት

ይህ ማለት ባል የሞተባትና በእርጅናዋ የሚረዳት ልጅ የሌላት ሴት ማለት ነው።

ልብ በል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አስታውስ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 16:13

የመጠለያ በዓል

የዚህ በዓል ሌሎች ስሞች፣ “የመገናኛው ድንኳን በዓል”፣ “የዳስ በዓል”፣ እና “የመሰብሰብ በዓል”። በመከር ጊዜ ገበሬዎች በመስኩ ላይ ጊዜያዊ መጠለያ ይሠሩ ነበር። ይህ በዓል የሚደረገው የዓመቱ መከር ከተሰበሰበ በኋላ ነበር።

ሰባት ቀን

“7 ቀን” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በበሮችህ ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮችህ” የሚለው ቃል የሚወክለው ከተሞችንና መንደሮችን ነው። “በመንደሮችህ ውስጥ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 16:15

በዓሉን

“የመጠለያ በዓሉን”

የእጆችህን ሥራ ሁሉ

እዚህ ጋ “እጆች” የሚወክሉት ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “የምትሠራውን ሥራ ሁሉ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 16:16

ወንዶችህ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት ይቅረቡ

እግዚአብሔር ሴቶቹ እንዲመጡ ባይጠይቅም ለእነርሱም ተፈቅዶላቸዋል። ወንዶቹ መላውን ቤተሰባቸውን መወከል ይችሉ ነበር።

በእግዚአብሔር ፊት ይቅረቡ

“ይምጡና በእግዚአብሔር ሀልዎት ፊት ይቁሙ”

ማንም በእግዚአብሔር ፊት ባዶ እጁን አይታይ

“በእግዚአብሔር ፊት ስጦታ ሳይዙ አይምጡ”። እነዚህ ሁለት አሉታዊ ሐረጎች በአንድ ላይ አዎንታዊ ትርጉም አላቸው። አ.ት፡ “ወደ እግዚአብሔር ፊት የሚመጣ ሁሉ ስጦታ ያምጣ” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 16:18

ዳኞችን አድርግ

“ዳኞችን ሹም” ወይም “ዳኞችን ምረጥ”

በከተሞችህ በሮች ውስጥ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚወክለው ከተማን ወይም መንደርን ነው። አ.ት፡ “በመንደሮችህ ሁሉ ውስጥ” (See: Synecdoche)

ይወሰዳሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ትመርጣቸዋለህ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በሕዝቡ ላይ በጽድቅ ፍርድ ዳኙ

“ሕዝቡን በፍትሐዊነት ዳኙ”

ፍትሕን በኃይል ምክንያት አታዛባ

ሙሴ ስለ ፍትሕ ሲናገር ብርቱው ሰው ከደካማው ሰው በጉልበት እንደሚቀማው አንዳች ቁሳዊ አካል አድርጎ ይናገራል። ይህ በአዎንታዊ መልኩ ሊነገር ይችላል። የአንተ ቋንቋ “ለመውሰድ ኃይል ተጠቀም” ለማለት አንድ ቃል ይኖረው ይሆናል። አ.ት፡ “በምትዳኝበት ጊዜ ኢፍትሐዊ አትሁን” ወይም “ትክክለኛ ውሳኔዎችን ስጥ” (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት and Double Negatives))

አታድርግ

እዚህ ጋ “አንተ” የሚያመለክተው እነዚያን ዳኞችና አለቆች ተደርገው የተሾሙትን ነው። (See: Forms of You)

ጉቦ የጠቢቡን ዓይኖች ያሳውራልና የጻድቁንም ቃል ያጣምማልና

ጉቦ መቀበል ሰዎችን እንደሚያበላቸው ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ጉቦን የሚቀበል ጥበበኛ ሰው እንኳን ይታወራል፣ ጉቦን የሚቀበል ጻድቅ ሰውም እንኳን ሐሰትን ይናገራል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ጉቦ የጠቢቡን ዓይኖች ያሳውራል

ክፉ በሆነው ነገር ላይ እንዳይናገር ጉቦን የሚቀበል ጠቢብ ሰው የሚታወር ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ጠቢቡ

“ጠቢቡ” የሚለው ስማዊ ቅጽል እንደ ቅጽል ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ጠቢብ ሰው” ወይም “ጥበበኛ ሰዎች” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

የጻድቁን ቃል ያጣምማል

“ጻድቅ” የሚለው ስማዊ ቅጽል እንደ ቅጽል ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ጻድቁን ሰው እንዲዋሽ ያደርገዋል” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

ፍትሕን ተከተል፣ ፍትሕን ብቻ ተከተል

ፍትሕ በሚራመድ ሰው ተመስሎ ተነግሮለታል። ትክክለኛና ቅን የሆነውን ነገር የሚያደርግ ሰው ፍትሕን በቅርበት እንደተከተለ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “አግባብነት ያለውን ብቻ አድርግ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አምላክህ እግዚአብሔር የሚሰጥህን ምድር ውረስ

እግዚአብሔር ለሕዝቡ የሚሰጣቸውን ምድር መቀበል ሕዝቡ ምድሪቱን ከእግዚአብሔር እንደሚወርስ ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 16:21

ማድረግ የለብህም

እዚህ ጋ “አንተ” የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ በሙሉ ነው። (See: Forms of You)

አምላክህ እግዚአብሔር የሚጠላውን የትኛውንም የድንጋይ ማምለኪያ ዐምድ

“አምላክህ እግዚአብሔር የሚጠላውን” የሚለው ሐረግ ስለ ማምለኪያ የድንጋይ ዐምድ የበለጠ መረጃ ይሰጣል። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር ስለሚጠላቸው የትኛውንም የማምለኪያ የድንጋይ ዐምድ” (See: Distinguishing versus Informing or Reminding)

የማምለኪያ የድንጋ ዐምድ

ይህ የሚያመለክተው ሐሰተኞችን አማልክት ለማምለክ የሚጠቀሙባቸውን ጣዖታት የሆኑ ዐምዶችን ነው።


Chapter 17

1 እንከን ወይም ጉድለት ያለበትን በሬ ወይም በግ እግዚአብሔር ለአምላክችሁ አትሠዉ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት አስጸያፊ ነውና። 2 እግዚአብሔር በሚሰጣችሁ ከተሞች በሮች አብሮአችሁ የሚኖር ወንድ ወይም ሴት ኪዳኑን በማፍረስ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ድርጊት ሲፈጽም ቢገኝ፥ 3 ትእዛዜንም በመተላለፍ ባዕዳን አማልክትን ያመለከ፥ ለእርሱም ማለትም ለፀሐይ ወይምለጨረቃ ወይም ለሰማይ ከዋክብት የሰገደ፥ 4 እናንተ ይህ መደረጉን ብትሰሙ ነገሩን በጥንቃቄ መርምሩ፥ የተባለውም እውነት ከሆንና እንዲህ ያለ አስጸያፊ ነገር በእስራኤል ዘንድ መፈጸሙ ከተረጋገጠ፥ 5 ይህን ክፉ ድርጊት የፈጸመውን ወንድ ወይም ሴት ወደ ከተማ ደጅ ወስዳችሁ ያን ሰው እስኪሞት ድረስ በድንጋይ ውገሩት። 6 ሞት የሚገባው ሰው በሁለት ወይም በሦስት ሰዎች ምስክርነት ይገደል፥ ነገር ግን በአንድ ሰው ምስክርነት ብቻ ማንም ሰው አይገደል። 7 ሲገደልም መጀመሪያ የምስክሮቹ እጅ ቀጥሎም የሕዝቡ ሁሉ እጅ ይረፍበት ክፉን ከመካከላችሁ አስወግዱ። 8 በአንድ የነፍስ ግድያ ዓይነትና በሌላ በአንድ ዓይነት ሕጋዊ ክርክርን በሌላ ወይም በአንድ የክስ ዓይነትና በሌላ መካከል ውሳኔ የሚጠይቅ ማንኛውም ጉዳይ ቢነሣ፥ ከአቅማችሁ በላይ የሆነ ጉዳይ በከተሞቻችሁ ውስጥ ቢያጋጥማችሁ፥ ተነሥታችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ ወደሚመርጠው ስፍራ ውጡ። 9 ካህናት ወደ ሆኑት ሌዋውያንና በዚያን ጊዜ ዳኛ ወደ ሆነው ሰው ሄዳችሁ ስለ ጉዳዩ ጠይቁአቸው፥ እነርሱም ውሳኔውን ይነግሩአችኋል። 10 እናንተም እግዚአብሔር በሚመርጠው ስፍራ እነርሱ በሚሰጡአችሁ ውሳኔ መሠረት ፈጽሙ። እንድፈጽሙ የሚሰጡአችሁን መመሪያ ሁሉ በጥንቃቄ አድርጉ፥ 11 በሚያስተምሩአችሁ ሕግና በሚሰጡአችሁ መመሪያዎች መሠረት ፈጽሙ፥ እነርሱ ከሚነግሩአችሁ ቀኝም ግራም አትበሉ። 12 እግዚአብሔር አምላካችሁን ለማገልገል በዚያ የሚቆመውን ካህን ወይም ዳኛ የሚንቅ ይገደል፥ ከእስራኤልም መካከል ክፉውን አስወግዱ። 13 ሕዝቡም ሁሉ ይህን ሲሰማ ይፈራል፤ ከዚያ ወዲያም እንዲህ ያለውን የንቀት ድርጊት አይደግመውም። 14 እግዚአብሔር አምላካችሁ ወደሚሰጣችሁ ምድር ስትገቡ፥ በምትወርሱአትና በምትቀመጡባት ምድር በዙርያዬ እንዳሉት አሕዛብ ሁሉ፥ እኔም በላዬ ንጉሥ ላንግሥ ብትሉ፥ 15 ከዚያ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ የሚመርጠውን ንጉሥ በላይህ ታነግሣለህ፥ ከገዛ ወንድሞችህ መካከል እንጂ እስራኤላዊ ወንድምህ ያልሆነውን ባዕድ በላይህ አታንግሥ። 16 ንጉሡም ብዙ ፈረሶችን ለራሱ አያብዛ ወይም ደግሞ የፈረሰኞችን ቁጥር ለመጨመር ሕዝቡን ወደ ግብፅ አይመልስ፤ 17 እግዚአብሔር በዚያ መንገድ ፈጽሞ አትመለሱ፥ ብሎአችኋልና፤ ልቡ እንዳይስትም ብዙ ሚስቶችን አያግባ፥ ብዙ ብር ወይም ወርቅ ለራሱ አያብዛ። 18 በመንግሥቱ ዙፋን ላይ በሚቀመጥበትም ጊዜ የዚህን ሕግ ቅጅ ከሌዋውያን ካህናት ወስዶ በጥቅልል መጽሐፍ ለራሱ ይጻፍ። 19 እግዚአሔር አምላኩን ማክበር ይማር ዘንድ የዚህን ሕግ ቃል ሁሉና ይህን ሥርዓት በጥንቅቄ ይጠብቅ ዘንድ ከእርሱ ጋር ይሁን፤በሁሉም ቀኖች ያንብበው። 20 ይህን የሚያደርገው ከወንድሞቹ ላይ ልቡ እንዳይኮራ፥ ከትእዛዘትም ወደ ኋላ እንዳይመለስ፥ እርሱና ልጆቹም ረጅም ዘመን ይገዙ ዘንድ፥ ከሕጉ ቀኝ ወይም ግራም አበል።



Deuteronomy 17:1

የትኛውም እንከን ያለበት

“እንከን ያለበት” ወይም “አንዳች ጉድለት ያለበትን”። እንስሳው ሲታይ ጤነኛና እንከን የሌለበት

ያ ለእግዚአብሔር አስጸያፊ ይሆናል

“ያ ለእግዚአብሔር አስቀያሚ ይሆናል

Deuteronomy 17:2

ቢገኝ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ብታገኝ” ወይም “አንድ ሰው ቢኖር” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በየትኛውም የከተማህ በሮች ውስጥ

እዚህ ጋ “የከተማ በሮች” ከተሞችን ወይም መንደሮችን ይወክላሉ። አ.ት፡ “ከከተሞችህ በአንዱ ቢኖር” (See: Synecdoche)

በአምላክህ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የእግዚአብሔርን ውሳኔ ወይም ምዘና ይወክላል። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር ክፉ ነው ብሎ የሚያስበው ነገር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቃል ኪዳኑን ይተላለፋል

“ቃል ኪዳኑን አይታዘዝም”

የትኛውንም የሰማይ ሰራዊት

“የትኛውንም ኮከብ”

እኔ ያላዘዝኩትን

“እንዲያደርገው ለማንም ያላዘዝኩትን”

ስለዚህ ነገር ቢነገርህ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ስለዚህ የእምቢተኝነት ተግባር ቢነግርህ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በጥንቃቄ መርምር

የነገር ስም የሆነው “ምርመራ” እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሆነውን ነገር በጥንቃቄ መርምር” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

እንዲህ ያለ አስጸያፊ ነገር በእስራኤል ተደርጎ እንደሆን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው እንዲህ ያለውን አስከፊ ነገር በእስራኤል አድርጎ እንደሆነ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 17:5

ሞት የሚገባው ሰው በሁለት ወይም በሦስት ምስክሮች አፍ ይገደል

እዚህ ጋ “አፍ” የሚወክለው የመስካሪዎችን ምስክርነት ነው። ይህ ወደ አድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በሰውየው ላይ ሁለት ወይም ሦስት ምስክሮች ከመሰከሩበት ከዚያ በኋላ ታስወግደዋለህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር፣ አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ እና ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ነገር ግን በአንድ ምስክር አፍ ብቻ መገደል የለበትም

እዚህ ጋ “አፍ” የሚወክለው የመስካሪውን ምስክርነት ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ነገር ግን በእርሱ ላይ የሚመሰክረው አንድ ሰው ብቻ ከሆነ ያንን ሰው ማስወገድ አይኖርብህም” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እርሱን ለመግደል በመጀመሪያ የምስክሮች እጅ፣ ከዚያም የሕዝቡ ሁሉ እጅ ይረፍበት

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ምስክሮችን በሙሉ ነው። አ.ት፡ “ድንጋዮቹን ለመወርወር ምስክሮቹ ራሳቸው የመጀመሪያ ይሁኑ፣ ከዚያም ሕዝቡ ሁሉ በእርሱ ላይ ድንጋይ በመወርወር ይግደሉት” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 17:8

ጉዳይ ቢነሣ

“ጉዳይ ቢኖር” ወይም “ሁኔታ ቢኖር”

የአንዱ ሰው መብትና የሌላው ሰው መብት

“መብት” አንድ ሰው አንድን ነገር የሚያደርግበት ወይም አንድ ነገር እንዲኖረው የሚያስችለው ሕጋዊ ስልጣን ነው።

በከተማህ በሮች ውስጥ

እዚህ ጋ “የከተማ በሮች” ከተሞችን ወይም መንደሮችን ይወክላል። አ.ት፡ “በመንደርህ ውስጥ” (See: Synecdoche)

ምክራቸውን ጠይቅ

የነገር ስም የሆነው “ምክር” እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እንዲመክሩህ ጠይቃቸው” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ውሳኔውን ይሰጡሃል

የነገር ስም የሆነው “ውሳኔ” እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በጉዳዩ ላይ ውሳኔ ይሰጣሉ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 17:10

የተሰጠህን ሕግ ተከተል

ካህናትና ዳኛው የሚወስኑትን የሚታዘዝ ሰው በአካሉ ከሕግ ኋላ እንደተከተለ ተደርጎ ተነግሯል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስለ ጉዳዩ ዳኛውና ካህናት የሚወስኑትን ታዘዝ” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 17:12

ካህኑን የማይሰማ -- ወይም ዳኛውን የማይሰማ

“ካህኑን የማይታዘዝ … ወይም ዳኛውን የማይታዘዝ

ከእስራኤል ክፉን ታርቃለህ

ስማዊ ቅጽል የሆነው “ክፉን” እንደ ቅጽል ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ይህንን ክፉ ነገር ያደረገውን ሰው ከእስራኤል መካክል ታስወግደዋለህ” ወይም “ይህንን ክፉ ሰው ግደለው” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

ሕዝቡ ሁሉ ሰምተው ይፈራሉ፣ ከእንግዲህም የዕብሪትን ተግባር አይፈጽሙም

ሕዝቡ የዕብሪት ተግባር የፈጸመው ሰው ስለመገደሉ በሚሰሙበት ጊዜ ይፈራሉ እነርሱ ራሳቸው የዕብሪትን ተግባር አይፈጽሙም እንደ ማለት ነው። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 17:14

ወደ ምድሪቱ በምትመጡበት ጊዜ

“በምትመጡበት” የሚለው ቃል “በምትሄዱበት” ወይም “ስትገቡ” ተብሎ ሊተረጎም ይችላል። (ሂድ እና ና የሚለውን ተመልከት)

‘በዙሪያዬ እንዳሉት ሕዝቦች በራሴ ላይ ንጉሥ አነግሣለሁ’ በምትልበት ጊዜ፣ ያን ጊዜ

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ ነው። ቀጥተኛ የሆነው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ተደርጎ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከዚያም በዙሪያህ ያሉ ሀገራት ሕዝቦች ንጉሥ እንዳላቸው አንተም እንዲኖርህ ትወስናለህ፣ ከዚያም” (በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ እና ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

በዙሪያዬ እንዳሉት -- በራሴ ላይ ንጉሥ አነግሣለሁ

ሙሴ እንደ አንድ ሰው ቆጥሮ የሚናገራቸው ሰዎች አሉት። ወደ ብዙ ቁጥር ተውላጠ ስም መተርጎም በይበልጥ የተለመደ ይሆናል። አ.ት፡ “በዙሪያችን … ለራሳችን እናነግሣለን” (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

ለራሴ ንጉሥ አነግሣለሁ

በእስራኤል ለአንድ ሰው እንደ ንጉሥ እንዲገዛቸው ሥልጣን መስጠታቸው ሕዝቡ ያንን ሰው ከእነርሱ በላይ ባለ ቦታ ላይ እንዳስቀመጡት ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በዙሪያዬ እንዳሉት ሕዝቦች ሁሉ

“በዙሪያዬ ያሉ ሕዝቦች”

ሀገራት ሁሉ

እዚህ ጋ “ሀገራት” የሚወክሉት በሀገራቱ ውስጥ የሚኖሩትን ሰዎች ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከወንድሞችህ መካከል አንዱን

“እንደ አንተው እስራኤላዊ ከሆኑት አንዱን”

በራስህ ላይ ወንድምህ ያልሆነውን መጻተኛ

የእነዚህ ሁለት ሐረጎች ትርጉም ተመሳሳይ ነው። ሁለቱም የሚያመለክቱት እስራኤላዊ ያልሆነውን ሰው ነው። የእስራኤል ሕዝብ መጻተኛው እንዲገዛቸው እንዳይፈቅዱ እግዚአብሔር አጽንዖት ሰጥቷል። አ.ት፡ “በራስህ ላይ መጻተኛውን” ወይም “እስራኤላዊ ያልሆነውን በራስህ ላይ” (See: Doublet)

Deuteronomy 17:16

እግዚአብሔር፣ ‘በዚያ መንገድ እንዳትመለስ’ ብሎአልና።

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ሌላ ትዕምርተ ጥቅስ አለው። ቀጥተኛው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ተደርጎ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ዳግመኛ ወደ ግብፅ እንዳትመለሱ ብሏልና” (በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ እና ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

ልቡ እንዳይስት

እዚህ ጋ “ልብ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። ባዕዳን ሴቶችን የሚያገባና የእነርሱን ሐሰተኛ አማልክት ለማምለክ የሚጀምር እስራኤላዊ ንጉሥ ልቡ ከእግዚአብሔር እንደሚመለስ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን ማክበሩን በማቆም ሐሰተኞች አማልክትን ማምለክ እንዲጀምር እንዳያደርጉት” (Synecdoche and ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 17:18

በመንግሥቱ ዙፋን ላይ በሚቀመጥበት ጊዜ

እዚህ ጋ “ዙፋን” የሚወክለው ሰውየው እንደ ንጉሥ የሚኖረውን ኃይልና ሥልጣን ነው። በዙፋን መቀመጥ ንጉሥ መሆን ማለት ነው። አ.ት፡ “ንጉሥ በሚሆንበት ጊዜ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የዚህን ሕግ ቅጅ ለራሱ በጥቅልል ላይ ይጻፈው

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፣ 1) “በግሉ የዚህን ሕግ ቅጅ በጥቅልል ላይ ለራሱ ይጻፍ” ወይም 2) “የዚህን ሕግ ቅጅ የሚጽፍለትን ሰው ይሹም”

ሌዋውያን በሆኑት ካህናት ፊት ካለው ሕግ

“ሌዋውያን ካህናት ከሚጠብቁት ከሕጉ ቅጅ”

የዚህን ሕግ ቃል ሁሉ እና እነዚህን ሥርዓቶች እንዲጠብቅ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች በመሠረቱ የሚሉት ተመሳሳይ ነገር ሲሆን ንጉሡ የእግዚአብሔርን ሕግ በሙሉ መታዘዝ እንዳለበት አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Parallelism)

Deuteronomy 17:20

ልቡ በወንድሞቹ ላይ እንዳይታበይ

እዚህ ጋ “ልቡ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። የአንድ ንጉሥ ዕብሪተኛ መሆን ልቡ እንደ ታበየ ሆኖ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “ዕብሪተኛ እንዳይሆን” ወይም “እንደ እርሱ ካለው እስራኤላዊ ይልቅ የተሻለ እንደሆነ እንዳያስብ” (Synecdoche እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከትዕዛዛቱ ወደ ቀኝ ወይም ወደ ግራ እንዳይመለስ

አንድ ንጉሥ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት አለመታዘዙ አንድ ሰው ከትክክለኛው መንገድ እንደሚወጣ በሚመስል መልኩ ተነግሯል። ይህ በአዎንታዊ መልኩ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከትዕዛዛቱ የትኛውንም ሳይታዘዝ እንዳይቀር” ወይም “ትዕዛዛቱን ሁሉ እንዲጠብቅ” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና ምጸት የሚለውን ተመልከት)


Chapter 18

1 ሌዋውን ካህናት፥ የሌዊ ነገድ ሁሉ ከእስራኤል ጋር የመሬት ድርሻ ወይም ርስት ስለማይኖራቸው ለእግዚአብሔር በእሳት የሚቀርበው ድርሻቸው ነውና ይብሉ። 2 እግዚአብሔር በሰጣቸው ተስፋ መሠረት እርሱ ራሱ ርስታቸው ስለሆነ በወንድሞቻቸው መካከል ርስት አይኖራቸውም። 3 ኮርማ ወይም በግ የሚሠዋው ሕዝብ ለካህኑ የሚሰጠው ድርሻ ወርቹን፥ ሁለት ጉንጮችንና የሆድ ዕቃውን ነው። 4 የእህላችሁን፥ የአዲሱን ወይናችሁንና የዘይታችሁን በኩራት እንዲሁም ከበጎቻችሁ በመጀመሪያ የተሸለተውን ጠጉር ትሰጣላችሁ። 5 በእግዚአብሔር ስም ቆሞ ለዘላለም ያገለግል ዘንድ እግዚአብሔር አምላክህ ከነገዶቻችሁ ሁሉ እርሱንና ዘሮቹን መርጦአል። 6 አንድ ሌዋዊ ከሚኖርበት ከየትኛውም በእስራኤል ካሉት ከተሞቻችሁ መካከል በፍጹም ፈቃድ እግዚአብሔር ወደሚመርጠው ስፍራ ቢመጣ፥ 7 በእግዚአብሔር ፊት ቆመው እንደሚያገለግሉት ሌዋውያን ወንድሞቹ፥ እርሱም በእዚግአብሔር በአምላኩ ስም ያገልግል። 8 ከቤተ ሰቡ ንብረት ሽያጭ ላይ ገንዘብ ቢቀበል እንኳ ባልንጀሮቹ ከሚያገኙት ጥቅም እኩል ይካፈላል። 9 እግዚአብሔር አምላካችሁ ወደሚሰጣችሁ ምድር በምትገቡበትጊዜ በዚያ የሚኖሩት አሕዛብ የሚፈጽሙትን አስጸያፊ መንገድ አትከተሉ። 10 በመካከላችሁ ወንድ ወይም ሴት ልጁን በእሳት የሚሥዋ ሟርተኛ፥ ወይም መተተኛ፥ ሞራ ገለጭ፥ ጠንቋይ፥ ወይም በድግምት የሚጠነቁል፥ 11 መናፍስት ጠሪ ወይም ሙት አነጋጋሪ በመካከላችሁ ከቶ አይገኝ። 12 እነዚህን የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ ነው፥ ከእነዚህ አጸያፊ ልምዶች የተነሣ እግዚአብሔር አምላካችሁ እነዚያን አሕዛብ ከፊታችሁ ያስወጣቸዋል። 13 በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ነውር የሌላው ይሁን። 14 ምድራቸውን የምታስለቅቃቸው አሕዛብ፥ መተተኞችን ወይም ሟርተኞችን ያዳምጣሉ፤ እናንተ ግን ይህን እንድታደርጉ እግዚአብሔር አምላካችሁ አልፈቀደላችሁም። 15 እግዚአብሔር አምላካችሁ ከገዛ ወንድሞቻችሁ መካከል እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሣላችኋል። እርሱን አድምጡ። 16 በኮሬብ ጉባኤ በተደረገበት ዕለት እንዳልሞት የእግዚአብሔር የአምላካችሁን ድምፅ አንስማ፤እንዲህ ያለውንም አስፈሪ እሳት ደግመን አንይ ብላችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁን የጠየቃችሁት ይህ ነውና። 17 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፥ የተናገሩት መልካም ነው። 18 ከወንድሞቻቸው መካከል እንደ አንተ ያለ ነቢይ አስነሣላቸዋለሁ። ቃሌን በአፉ አደርጋለሁ፤ የማዘውንም ሁሉ ይነግራቸዋል። 19 ማንም ሰው ነቢዩ በስሜ የሚናገረውን ቃሌን ባይሰማ፤ እኔ ራሴ ተጠያቂነት አደርገዋለሁ። 20 ነገር ግን እንዲናገር እኔ ያላዘዝሁትን ቃል በድፍረት በስሜና በሌሎች አማልክት ስም የሚናገር ነቢይ ይገደል። 21 እናንተም በልባችሁ እግዚአብሔር ያልተነገረውን መልእክት እንዴት ማወቅ እንችላለን? ብትሉ፥ 22 ነቢዩም በእግዚአብሔር ስም የተናገርው ካልተፈጸመ ወይም እውነት ሆኖ ካልተገኘ፤ መልእክቱ እግዚአብሔር የተናገርው አይደለም። ያ ነቢይ በድፍረት ተናግሮታልና እርሱን አትፍራው።



Deuteronomy 18:1

ከእስራኤል ጋር ድርሻም ሆነ ርስት አይኖራቸውም

ሌዋውያን የትኛውንም መሬት ከእግዚአብሔር አለመቀበላቸው ርስት እንዳልተቀበሉ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ከሕዝቡ መሬት የትኛውንም አይወስዱም” ወይም “እስራኤላውያን ከሚወስዱት መሬት የትኛውንም አይቀበሉም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ምንም ድርሻ

“ምንም ክፍል” ወይም “ምንም ድርሻ”

በወንድሞቻቸው መካከል

“በሌሎች የእስራኤል ነገዶች መካከል” ወይም “በሌሎች እስራኤላውያን መካከል”

ርስታቸው እግዚአብሔር ነው

አሮንና የእርሱ ተወላጆች እንደ ካህናት እግዚአብሔርን በማገልገላቸው ታላቅ ክብር እንደሚኖራቸው ሙሴ ሲናገር እግዚአብሔርን እንደሚወርሱት አንዳች ነገር አድርጎ ይናገራል። ተመሳሳዩን ሐረግ በዘዳግም 10፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ከዚያ ይልቅ እግዚአብሔር ይኖራቸዋል” ወይም “ከዚያ ይልቅ፣ እግዚአብሔር እርሱን እንዲያገለግሉት ይፈቅድላቸዋል፣ በዚያም አገልግሎት የሚያስፈልጋቸውን ያቀርብላቸዋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 18:3

በውስጥ ያሉትን ክፍሎች

ይህ ጨጓራና አንጀት ነው።

ትሰጠዋለህ

“ለካህኑ ትሰጠዋለህ”

መርጦታል

እዚህ ጋ “እርሱን” ሌዋውያንን ሁሉ ይወክላል። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእግዚአብሔር ስም ለማገልገል እንዲቆም

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ስም” የቆመው ለራሱ ለእግዚአብሔርና ለሥልጣኑ ነው። አ.ት፡ “የእርሱ ልዩ አገልጋዮች እንዲሆኑ” ወይም “እንደ እግዚአብሔር ተወካዮች እንዲያገለግሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እርሱንና ወንዶች ልጆቹን ለዘላለም

እዚህ ጋ “እርሱን” የሚወክለው ሌዋውያንን ሁሉ ነው። አ.ት፡ “ሌዋውያንና ተወላጆቻቸው ለዘላለም” (See: Synec- doche)

Deuteronomy 18:6

በሙሉ ነፍሱ ቢፈልግ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በብርቱ ቢፈልግ” ወይም “በእርግጠኝነት ቢፈልግ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም በአምላኩ በእግዚአብሔር ስም ያገልግል

እዚህ ጋ “ስም” የሚወክለው እግዚአብሔርን እና የእርሱን ሥልጣን ነው። አ.ት፡ “ከዚያም አምላኩን እግዚአብሔርን በካህንነት ያገልግል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእግዚአብሔር ፊት በዚያ የሚቆሙት

“በእግዚአብሔር ሀልዎት ፊት በመቅደሱ የሚያገለግሉት”

የቤተሰቡን ርስት

ካህኑ ከአባቱ የሚወርሰው ይህ ነው

Deuteronomy 18:9

በምትመጣበት ጊዜ

(ሂድ እና ና የሚለውን ተመልከት)

የእነዚያን ሕዝቦች አስጸያፊ ተግባር ለመጠበቅ አትማር

በዙሪያቸው ያሉትን ሀገራት ሰዎች ሃይማኖታዊ ተግባራት እግዚአብሔር ይጠላል። እርሱ እጅግ ክፉዎች እንደሆኑ አድርጎ ይመለክታቸዋል። እዚህ ጋ “ሀገሮች” ሰዎቹን ይወክላሉ። አ.ት፡ “የሌሎች ሀገራት ሰዎች የሚያደርጓቸውን አስከፊ ነገሮች አታድርጉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በመካከልህ ማንም አይገኝ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በመካከልህ ማንም አይኑር” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ማንም የሚጠነቁል -- ከመናፍስት ጋር የሚነጋገር

እነዚህ አስማትን የሚለማመዱ የተለዩ ሰዎች ናቸው። የትኛውንም ዓይነት አስማት እግዚአብሔር ከልክሏል። ለእንደዚህ ዓይነቶቹ ሰዎች ሁሉ የሚሆን ቃል ከሌለህ በይበልጥ ጥቅል በሆነ መልኩ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ወደፊት የሚሆነውን ለማወቅ በመሞከር፣ ዕጣ ለመጣል ወይም የሙታንን መናፍስት ለማነጋገር አስማት የሚጠቀም ማንም ቢሆን”

በሲኒ የሚገኙ ምልክቶችን የሚያነብ

በሲኒ ውስጥ ያሉ ቅርጾችንና ስዕሎችን የሚያነብና ከሚያየው ተነሥቶ ወደፊት የሚሆኑትን ሁነቶች የሚተነብይ

Deuteronomy 18:12

ያባርራቸዋል

እዚህ ጋ “እነርሱን” የሚያመለክተው አስቀድሞ በከነዓን የሚኖሩትን ሰዎች ነው።

ለእነዚህ ሕዝቦች

እዚህ ጋ “ሕዝቦች” የሚለው ቃል የቆመው በከነዓን ለሚኖሩ የሕዝብ ወገኖች ነው። አ.ት፡ “ለእነዚህ የሕዝብ ወገኖች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የምታስወጧቸውን እነዚህን ሕዝቦች

“መሬታቸውን የምትወስድባቸው እነዚህ ሕዝቦች”

Deuteronomy 18:15

አምላክህ እግዚአብሔር ነቢይ ያስነሣልሃል

ነቢይ እንዲሆን እግዚአብሔር አንድን ሰው መሾሙ እግዚአብሔር ሰውየውን እንደሚያነሣው ወይም ብድግ እንደሚያደርገው ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከወንድሞችህ አንዱ

“እንዳንተው እስራኤላዊ ከሆኑት አንዱ”

የጠየቅኸው ይህንን ነው

እዚህ ጋ “አንተ” የሚያመለክተው ከ40 ዓመታት በፊት በኮሬብ ተራራ የነበሩትን እስራኤላውያንን ነው።

በኮሬብ ጉባዔ በተደረገበት ቀን

“በኮሬብ በአንድ ላይ በተሰበሰባችሁበት ቀን”

ጉባዔ በተደረገበት ቀን፣ ‘የአምላካችንን የእግዚአብሔርን ድምፅ አንስማ፣ ይህንን ታላቅ እሳትም ከእንግዲህ አንይ፣ እንዲህ ካልሆነ እንሞታለን’ ስትል

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ ነው። ቀጥተኛ የሆነው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ተደርጎ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ጉባዔ በተደረገበት ቀን እንዳትሞት ፈርተህ ስለነበር የአምላካችንን የእግዚአብሔርን ድምፅ መስማትም ሆነ ከእንግዲህ የእርሱን ታላቅ እሳት ማየት እንደማትፈልግ በተናገርክ ጊዜ” (በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ እና ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

የአምላካችንን የእግዚአብሔርን ድምፅ እንደገና አንስማ

እዚህ ጋ እግዚአብሔር ለተናገረው አጽንዖት ለመስጠት የእርሱ በሆነ ”ድምፅ” ተወክሏል። አ.ት፡ “አምላካችን እግዚአብሔር እንደገና ሲናገር አንስማ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 18:17

ነቢይ አስነሣላቸዋለሁ

እግዚአብሔር፣ አንድን ሰው ነቢይ እንዲሆን መሾሙ፣ እግዚአብሔር ሰውየውን እንደሚያነሣው ወይም ብድግ እንደሚያደርገው ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከወንድሞቻቸው መካከል

“እንደ እነርሱ እስራኤላዊ ከሆኑት መካከል”

ቃሌን በአፉ ላይ አኖራለሁ

ነቢዩ ምን ማለት እንዳለበት እግዚአብሔር ለእርሱ መንገሩ እግዚአብሔር በነቢዩ አፍ ውስጥ ቃልን እንደሚጨምርበት ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ይነግራቸዋል

“ለእስራኤል ሕዝብ ይነግራቸዋል”

በስሜ የሚናገረውን ቃል የማይሰማ

እዚህ ጋ “ስሜ” የሚወክለው እግዚአብሔርን እና ሥልጣኑን ነው። አ.ት፡ “መልዕክቴን በሚናገርበት ጊዜ የማይሰማው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እጠይቀዋለሁ

“በኃላፊነት እጠይቀዋለሁ” ወይም “እቀጣዋለሁ”። እዚህ ጋ “እርሱን” የሚያመለክተው ነቢዩን የማይሰማውን ሰው ነው።

Deuteronomy 18:20

በትዕቢት ቃልን የሚናገር

“መልዕክት ለመናገር የሚደፍር” ወይም “በዕብሪተኝነት መልዕክት የሚናገር”

በስሜ

እዚህ ጋ “ስሜ” የሚያመለክተው ራሱን እግዚአብሔርንና ሥልጣኑን ነው። አ.ት፡ “ለእኔ” ወይም “በእኔ ሥልጣን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቃልን

“መልዕክትን”

በሌሎች አማልክት ስም የሚናገር

እዚህ ጋ “ስም” የሚወክለው አማልክቱን ራሳቸውን ወይም ሥልጣናቸውን ነው። ይህ ማለት ሐሰተኞቹ አማልክት አንድን መልዕክት እንዲናገር እንደ ነገሩት ነቢዩ ያስታውቃል ማለት ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በልብህ እንዲህ ትላለህ

እዚህ ጋ “ልብ” የሚወክለው የሰውን አሳብ ነው። አ.ት፡ “ራስህን ትጠይቃለህ” ወይም “ለራስህ ትናገራለህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መልዕክቱን እግዚአብሔር እንዳልተናገረ እንዴት እንለያለን?

“ነቢዩ የሚናገረው መልዕክት ከእግዚአብሔር መሆኑን እንዴት እናውቃለን? እዚህ ጋ “እኛ” የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው።

Deuteronomy 18:22

ነቢይ የሚናገረው በእግዚአብሔር ስም ነው

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ስም” የሚያመለክተው ራሱን እግዚአብሔርን እና ሥልጣኑን ነው። አ.ት፡ “ነቢይ እኔን ወክሎ እንደሚናገር ያስታውቃል” ወይም “ነቢይ በእኔ ሥልጣን እንደሚናገር ያስታውቃል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ነቢዩ በማንአለብኝነት ተናግሮታል

“ነቢዩ ይህንን መልዕክት የተናገረው ያለ እኔ ሥልጣን ነው”


Chapter 19

1 እግዚአብሔር አምላካችሁ ምድራቸውን ለእናንተ የሚሰጥባቸውን አሕዛብ በሚደመስሳቸው ጊዜና እናንተም እነርሱን አስለቅቃችሁ በከተሞቻቸውና በቤቶቻቸው በምትቀመጡበት ጊዜ፥ 2 እግዚአብሔር አምላካችሁ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ ምድር አማካይ ስፍራ ሦስት ከተሞችን ለራሳችሁ ምረጡ፥ 3 ሰው የገደለ ሁሉ እንዲሸሽባቸው እግዚአብሔር አምላካችሁ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ ምድር መንገዶችን ሠርታችሁ በሦስት ክፈሉአቸው። 4 በተንኮል ሳይሆን ድንገት ሳያስበው ባልንጀራውን ገድሎ ሕይወቱን ለማትረፍ ለሚሸሽ ሰው መመሪያው የሚከተለው ነው። 5 እነሆ፥ አንድ ሰው ከባልንጀራው ጋር እንጨት ለመቁረጥ ወደ ጫካ ቢሄድ፥ ዛፉን ለመጣል መጥረቢያውን በሚሰነዝርበት ጊዜ ብረቱ ከእጀታው ወልቆ ባልንጀራውን በመምታት ቢገድለው፥ ያ ሰው ከእነዚህ ከተሞች ወደ አንዱ በመሸሽ ሕይወቱን ማትረፍ ይችላል። 6 አለበለዚያ በተንኮል ሳይሆን ድንገት ሳያስበው ባልንጀራውን ቢገድል፥ መንገዱ ረጅም ከሆነ ደም ተበቃዩ በንዴት ተከታትሎ ይደርስበትና መገደል የማይገባውን ሰው ሊገድል ይችላል። ይህ ከመሆኑ በፊት ባልንጀራውን ያልጠላ ከሆነ መሞት አይገባውም። 7 ሦስት ከተሞችን ለራሳችሁ እንድትመርጡ ያዘዙአችሁ በዚሁ ምክንያት ነው። 8 ለአባቶቻችሁ በመሐላ በገባላቸው ቃል መሠረት አምላካችሁ እግዚአብሔር ወሰናችሁን ሲያሰፋውና ለእነርሱ በሰጣቸው መሠረት ምድሪቷን ሁሉ ሲሰጣችሁ፤ 9 እግዝክአብሔር አምላካችሁን እንድትወዱና ምን ጊዜም በመንገዱ እንድትሄዱ ዛሬ የማዛችሁን እነዚህን ሕግጋት ሁሉ በጥንቃቄ የምትጠብቁ ከሆነ በእነዚህ ላይ ሌሎች ሦስት ከተሞችን ትጨምራላችሁ። 10 እግዚአብሔር አምላካችሁ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ ምድር የንጹሕ ሰው ደም እንዳይፈስና በሚፈሰውም ደም በደለኛ እንዳትሆኑ ይህን አድርጉ። 11 ነገር ግን አንድ ሰው ባልንጀራውን ቢጠላው አድፍጦ ጥቃት ቢያደርስበት፥ ቢገድለውና ከእነዚህ ከተሞች ወደ አንዲቱ ቢሸሽ፥ 12 የሚኖርባት ከተማ ሽማግሌዎች ሰው ልከው ከከተማው ያስመጡት፥ እንዲገድለውም ለደም ተበቃዩ አሳልፈው ይስጡት። 13 አትራራለት፥ ነገር ግን መልካም እንዲሆንላችሁ የንጹሑን ደም በደል ከእስራኤል አስወግዱ። 14 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንድትወርሱአት በሚሰጣችሁ ምድር ውስጥ ለእናንተ በሚተላለፍላችሁ ርስት ላይ የቀድሞ ሰዎች ያስቀመጡትን የባልጀራችሁን የድንበር ምልክት አታንሡ። 15 በማንኛውም ወንጀል ወይም ሕግ በመተላለፍ ሰውን ጥፋተኛ ለማድረግ አንድ ምስክር አይበቃም፥ጉዳዩ በሁለት ወይም በሦስት ሰዎች ምስክርነት መረጋገጥ አለበት። 16 ተንኮለኛ የሆነ ምስክር አንድን ሰው በሐሰት ለመመስከር ቢነሣ፤ 17 ክርክሩ የሚመለከታቸው ሁለቱ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት በዚያ ወቅት በሚያገለግሉት ካህናትና ፈራጆች ፊት ይቁሙ። 18 ፈፋጆችም ጉዳዩን በጥልቅ ይመርምሩት፥ 19 ያም ምስክሩ በወንድሙ ላይ በሐሰት የመሰከረ መሆኑ ከተረጋገጠ በወንድሙ ላይ ለማድረግ ያሰበውን በእርሱ ላይ አድርጉበት ክፉውን ከመካከላችሁ አስወግዱ። 20 የቀሩትም ሰዎች ይህን ሰምተው ይፈራሉ፤ እንዲህ ያለው ክፉ ነገርም ለወደፊቱ በመካከላችሁ ከቶ አይደገምም። 21 ርኅራኄ አታድርጉ ሕይወት ለሕይወት፥ ዐይን ለዐይን፥ ጥርስ ለጥርስ፥ እጅ ለእጅ፥ እግር እግር ይመለስ።



Deuteronomy 19:1

አምላክህ እግዚአብሔር ሕዝቦችን በሚቆርጣቸው ጊዜ

እግዚአብሔር በከነዓን የሚኖሩትን ሰዎች ማጥፋቱ አንድ ሰው የጨርቅ ቁራጭ ወይም የዛፍ ቅርንጫፍ እንደሚቆርጥ እርሱም እንደሚቆርጣቸው ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሕዝቦችን

ይህ በከነዓን የሚኖሩትን የሕዝብ ወገኖች ይወክላል። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አምላክህ እግዚአብሔር ምድራቸውን የሚሰጥህን የእነዚያን

“አምላክህ እግዚአብሔር በሚሰጥህ ምድር ላይ ይኖሩ የነበሩት እነዚያ ሕዝቦች”

በምትመጣባቸው

“ከነዚያ ሕዝቦች ምድሪቱን ስትወስድ” ወይም “እነዚያ ሕዝቦች ከለቀቁ በኋላ ምድሪቱን የራስህ ስታደርግ”

ሦስት ከተሞችን ምረጥ

“3 ከተሞችን ምረጥ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

መንገድ ሥራ

ሰዎች ወደ እነዚህ ከተሞች ለመጓዝ እንዲቀላቸው መንገዶችን መሥራት ይኖርባቸዋል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

የምድርህን ድንበሮች በሦስት ቦታ ክፈላቸው

ከሚመርጧቸው ከተሞች አንዱ በእያንዳንዱ የምድሪቱ ክፍል ውስጥ ይሁን። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

አምላክህ እግዚአብሔር በሚያወርስህ ምድር

እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ ምድሪቱን መስጠቱ ሕዝቡ ምድሪቱን እንደወረሱ ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 19:4

ሕጉ ይህ ነው

“መመሪያዎቹ እነዚህ ናቸው” ወይም “አቅጣጫዎቹ እነዚህ ናቸው”

ሌላውን የገደለ

“ሰው” የሚለው ቃል እንዳለበት ይታወቃል። አ.ት፡ “ሌላውን ሰው የገደለ ሰው” (See: Ellipsis)

ወደዚያ የሚሸሽ

“ከእነዚህ ከተሞች ወደ አንዱ የሚያመልጥ” ወይም “ከእነዚህ ከተሞች ወደ አንዱ የሚሮጥ”

ለመኖር

“ሕይወቱን ለማዳን”። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የሟች ቤተሰብ ተበቅለው እንዳይገድሉት” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ማንም ሳያውቅ ባልንጀራውን የሚገድል

እዚህ ጋ “ባልንጀራ” ማለት በአጠቃላይ የትኛውም ሰው ማለት ነው። አ.ት፡ “በድንገት ሌላውን ሰው የሚገድል የትኛውም ሰው”

አስቀድሞ ጥላቻ ሳይኖረው

“ነገር ግን ባልንጀራውን ከመግደሉ በፊት አልጠላው እንደሆነ”። ባልንጀራውን አስቦበት የሚገድልበት ምክንያት እንዳልነበረው ያመለክታል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ለምሳሌ፣ አንድ ሰው እንጨት ለመቁረጥ ወደ ጫካ ቢሄድ

ደራሲው አንድ ሰው ሌላውን በድንገት የሚገድልበትን መላ ምታዊ ሁኔታ ይሰጣል። (See: Hypothetical Situations)

ብረቱ ከእጀታው ወልቆ

የመጥረቢያው የብረት ክፍል ከእንጨቱ እጀታ ወልቆ

ባልንጀራውን መትቶ ቢገድለው

ይህ ማለት የመጥረቢያው ራስ ባልንጀራውን መትቶ ገድሎታል ማለት ነው።

ከእነዚህ ከተሞች ወደ አንዲቱ -- ሕይወቱን ያድን

የሟቹ ሰው ቤተሰብ ምናልባት ሊበቀሉት እንደሚሞክሩ ያመለክታል። በዚያ ያሉት ሰዎች ጥበቃ እንዲያደርጉለት እርሱን የገደለው ሰው ከእነዚህ ከተሞች ወደ አንዲቱ መሸሽ ይችላል (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 19:6

ደም ተበቃዩ

እዚህ ጋ “ደም” የሚወክለው የተገደለውን ሰው ነው። “ደም ተበቃዩ” ሰው የሟቹ የቅርብ ዘመድ ነው። ገዳዩን ለመቅጣት ኃላፊነቱ የዚህ ዘመድ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሕይወትን የሚያጠፋ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ሌላውን ሰው የገደለ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በንዴት ግሎ

የአንድ ሰው በጣም መቆጣት ልክ ቁጣ እንደሚግል አንዳች ነገር ተቆጥሮ ተነግሯል። አ.ት፡ “በጣም ተቆጥቶ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ይመታውና ይገድለዋል

"ደም ተበቃዩ ሟችን የገደለውን ሰው ይመታና ይገድለዋል”

አስቀድሞ ባልንጀራውን አልጠላውምና ያ ሰው መሞት የሚገባው ባይሆንም

“ሌላውን ሰው የገደለው በድንገት ስለሆነና ጠላቱ ስላልነበረ፣ ሰውየውን ለመጉዳትም ስላላቀደ ያ ሰው መሞት የሚገባው ባይሆንም”

Deuteronomy 19:8

ድንበርህን ያሰፋል

“የምትወርሰውን ተጨማሪ መሬት ይሰጥሃል”

ለቅድም አያቶችህ እንደማለው

“እርሱ እንደሚያደርገው ለቅድም አያቶችህ ተስፋ የሰጠውን”

ታደርጋቸው ዘንድ እነዚህን ትዕዛዛት በሙሉ ብትጠብቅ

“እነዚህን ትዕዛዛት በሙሉ ብትታዘዝ”

ዘወትር በመንገዶቹ እንድትሄድ

እግዚአብሔር፣ አንድ ሰው እንዲኖረውና እንዲያደርገው የሚፈልግበት አግባብ እንደ እግዚአብሔር መንገድ ወይም ጎዳና ተቆጥሮ ተነግሯል። እግዚአብሔርን የሚታዘዝ ሰው በእግዚአብሔር መንገድ ወይም ጎዳና እንደ ሄደ ተቆጥሮ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “ዘወትር እንድትታዘዘው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም ሦስት ተጨማሪ ከተሞችን ለራስህ ትጨምራለህ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከዚያም አንድ ሰው በድንገት ሌላውን ሰው ከገደለ እንዲያመልጥበት ተጨማሪ ሦስት ከተሞችን ትመርጣለህ” (ቁጥሮች እና Assumed Knowl- edge and Implicit Information የሚለውን ተመልከት)

ከእነዚህ ከሦስቱ በተጨማሪ

“አስቀድሞ ካዘጋጀኻቸው ከሦስቱ ከተሞች በተጨማሪ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕ ደም እንዳይፈስ ይህንን አድርግ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የቤተሰቡ አባላት ንጹሕ የሆነውን ሰው እንዳይገድሉ ይህንን አድርግ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕ ደም እንዳይፈስ

እዚህ ጋ “ደም” የሚወክለው የሰውን ሕይወት ነው። ደም ማፍሰስ ማለት ሰው መግደል ማለት ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማንም ንጹሕ የሆነውን ሰው አይግደል” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በምድሪቱ መካከል

“በምድሪቱ” ወይም “በግዛቱ”

አምላክህ እግዚአብሔር ርስት አድርጎ በሚሰጥህ

እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ የሚሰጣቸው ምድር ርስት እንደሆነ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የደም በደለኛ እንዳትሆን

የእስራኤል ሕዝብ “ከደም ተበቃዩ” የሚያመልጥበትን ከተማ ባለመሥራታቸው በሚሞተው ሰው ምክንያት በደለኛ መሆናቸው የሟቹ በደል በእነርሱ ላይ እንደሚሆን ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የደም በደል

እዚህ ጋ “ደም” የሚወክለው ሕይወትን ሲሆን “የደም በደለኛ” የሚያመለክተው አንድ ሰው ንጹሕ የሆነን ሰው ስለ መግደሉ የሚኖርበትን በደል ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በአንተ ላይ እንዳይሆን

ይህ ማለት አንድ የቤተሰብ አባል ንጽሕ የሆነን ሰው ቢገድል፣ ከዚያም ይህ እንዲሆን ዝም በማለታቸው የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ በደለኛ ይሆናሉ።

Deuteronomy 19:11

ባልንጀራውን

እዚህ ጋ “ባልንጀራ” ማለት በአጠቃላይ ማንኛውም ሰው ማለት ነው።

አድፍጦ ቢጠብቀው

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እርሱን ለመግደል ተደብቆ ይጠብቀዋል” ወይም “ሊገድለው ያቅዳል” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

በእርሱ ላይ ይነሣል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ያጠቃዋል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እስኪሞት ድረስ ክፉኛ ቢያቆስለው

“እስኪሞት ድረስ ቢጎዳው” ወይም “ቢገድለው”

ልከው ከዚያ መልሰው ያምጡት

“እንዲያመጡት ሰው ይላኩ፣ እርሱንም ከተከለለበት ከተማ መልሰው ያምጡት”

አሳልፈው ይስጡት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አሳልፈው ይስጡት” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ኃላፊነት ባለበት ዘመዱ እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው የአንድን ሰው ሥልጣን ነው። አ.ት፡ “ኃላፊነት ላለበት ዘመዱ ሥልጣን” ወይም “ኃላፊነት ላለበት ዘመዱ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ኃላፊነት ያለበት ዘመድ

ይህ የተገደለው ሰው ዘመድ ነው። ይህ ዘመድ ገዳዩን ለመቅጣት ኃላፊ ነው።

እንዲሞት

“ገዳዩ እንዲሞት” ወይም “ኃላፊነት ያለበት ዘመድ ገዳዩን እንዲገድለው”

ዐይንህ አይራራለት

እዚህ ጋ “ዐይንህ” የሚወክለው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “ምሕረት አታድርግለት” ወይም “አትዘንለት” (See: Synecdoche)

የደምን በደል ከእስራኤል አስወግድ

እዚህ ጋ “የደም በደል” የሚወክለው ንጹሕ የሆነውን ሰው የመግደልን በደል ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ሕዝብ በንጹሕ ሰው ሞት ምክንያት በደለኛ እንዳይሆን ነፍሰ ገዳዩን ግደለው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእስራኤል

እዚህ ጋ “እስራኤል” የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 19:14

የባልንጀራህን የድንበር ምልክት አታንሣ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በመሬቱ ድንበር ላይ ያለውን ምልክት በማንሣት ከባልንጀራህ መሬት አትውሰድበት” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ያስቀመጡትን

“የቀደሙት አባቶችህ ያስቀመጡትን”

ከብዙ ዓመታት በፊት

ሙሴ ይህንን የሚለው ሕዝቡ ለረጅም ዓመታት በምድሪቱ በተቀመጡ ጊዜ የቀደሙት አባቶቻቸው በመጀመሪያ ምድሪቱን በወሰዱ ጊዜ ያበጁትን ድንበር እንዳያነሡ ነው።

አምላክህ እግዚአብሔር እንድትወርሰው በሚሰጥህ ምድር፣ በምትወርሰው ርስትህ

እግዚአብሕር ለእስራኤል ሕዝብ መሬት መስጠቱ ምድሪቱን እንደወረሱ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር እንድትወርሰው በሚሰጥህ ምድር” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 19:15

አንድ ብቸኛ ምስክር

“ አንድ ምስክር” ወይም “አንድ ምስክር ብቻ”

በሰው ላይ እንዳይነሣ

እዚህ ጋ “መነሣት” ማለት በፍርድ ቤት መቆምና አንድን ሰው በመቃወም ለዳኛው መናገር ማለት ነው። አ.ት፡ “አንድ ሰው ስላደረገው ክፉ ነገር ለዳኞች እንዳይናገር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ኃጢአት በሚሠራበት በየትኛውም ጉዳይ

አንድ ሰው በየትኛውም ጊዜ ክፉ ነገር ሲያደርግ”

በሁለት ምስክሮች አፍ ወይም በሦስት ምስክሮች አፍ

እዚህ ጋ “አፍ” የሚወክለው ምስክሮች የሚናገሩትን ነው። ቢያንስ ሁለት ወይም ሦስት ምስክሮች መኖር እንዳለባቸው ያመለክታል። አ.ት፡ “በሁለት ወይም በሦስት ሰዎች ምስክርነት” ወይም “ቢያንስ ሁለት ወይም ሦስት ሰዎች ተፈጽሟል ያሉትን መሠረት በማድረግ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Assumed Knowledge and Implicit Information የሚለውን ተመልከት)

የትኛውም ጉዳይ መረጋገጥ አለበት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሰውየው በደለኛ መሆኑን ታረጋግጣለህ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ቢሆን

“መቼ” ወይም “ከሆነ”

ሐሰተኛ ምስክር

“አንድን ሰው ለመጉዳት የሚሞክር ምስክር”

በማንም ላይ ክፉ ስለማድረጉ ሊመሰክርበት የሚነሣ

እዚህ ጋ “መነሣት” ማለት ፍርድ ቤት ውስጥ መቆምና አንድን ሰው በመቃወም ለዳኛው መናገር ማለት ነው። አ.ት፡ “ሰውየውን ችግር ላይ ለመጣል ኃጢአት ሠርቷል ብሎ ለዳኛው የሚናገር” ወይም “ዳኛው እንዲቀጣው አንድን ሰው ኃጢአት ሠርቷል ብሎ ለዳኛው የሚናገር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 19:17

ክርክር በመካከላቸው ያለ

“እርስ በእርስ ያልተስማሙ”

በእግዚአብሔር ፊት ይቁሙ፣ በካህናቱና በዳኞቹ ፊት

ይህ ማለት ሁለቱ ሰዎች የእግዚአብሔር ሀልዎት ወደሚያድርበት ቅዱስ ስፍራ መሄድ አለባቸው ማለት ነው። ስለ እግዚአብሔር ሕጋዊ ውሳኔዎችን የመስጠት ሥልጣን ያላቸው ካህናትና ዳኞች በተቀደሰው ስፍራ አሉ። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

በእግዚአብሔር ፊት ይቁሙ፣ በካህናቱና በዳኞቹ ፊት

“ፊት ይቁሙ” የሚለው ሐረግ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ይህ ማለት ሥልጣን ወዳለው አካል መሄድና እርሱ ስለ ጉዳዩ ሕጋዊ ውሳኔ እንዲሰጥ ማድረግ ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ዳኞቹ በጥንቃቄ ይመርምሩ

“ዳኞቹ የሆነውን ነገር ለማወቅ ጠንክረው መሥራት አለባቸው”

ከዚያም በወንድሙ ላይ ለማድረግ የተመኘውን በእርሱ ላይ ታደርግበታለህ

“ከዚያም ሐሰተኛውን ምስክር ሌላውን ሰው እንድትቀጣ በፈለገበት መንገድ ትቀጣዋለህ”

ክፉን ከመካከልህ ታስወግዳለህ

ስማዊ ቅጽል የሆነው “ክፉን” እንደ ቅጽል ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ክፉውን ልምምድ ከመካከልህ ታርቃለህ” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 19:20

ከዚያም የቀሩት

“ሐሰተኛውን ምስክር በምትቀጣበት ጊዜ የቀረው ሕዝብ”

ሰምተው ይፈራሉ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ስለ ቅጣቱ ይሰሙና እነርሱም እንዳይቀጡ ይፈራሉ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

እንዲህ ያለውን ክፉ ከእንግዲህ አይፈጽሙም

“እንደዚህ ያለውን ክፉ ነገር ደግመው አያደርጉም”

ዐይኖችህ አይራሩለት

እዚህ ጋ “ዐይኖች” የሚያመለክቱት ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “አትራራለት” ወይም “ምሕረት አታድርግለት” (See: Synecdoche)

ሕይወት ስለ ሕይወት ይከፈል -- እግር ስለ እግር

እዚህ ጋ ትርጉሙ ግልጽ ስለሆነ ሐረጎቹ አጥረዋል። ይኸውም አንድ ሰው ሌላውን ሰው በጎዳበት በዚያው መልኩ ሕዝቡ ይቀጣዋል ማለት ነው። (See: Ellipsis)


Chapter 20

1 ጠላቶቻችሁን ለመውጋት ወደ ጦርነት ስትሄዱ ሠርገሎችንና ፈረሶችን ከእናንተ የሚበልጥ ሰራዊትንም በምታዩበት ጊዜ፥ አትፍሩአቸው፥ ከግብፅ ያወጣችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ ከእናንተ ጋር ነውና። 2 ወደ ውጊያው ቦታ ስትቃረቡ፥ 3 ካህኑ ወደ ፊት ወጣ ብሎ ለሠራዊቱ ይናገር፥ እንዲህም ይበል እስራኤል ሆይ ስማ በዛሬው ቀን ጠላቶቻችሁን ለመግጠም ወደ ጦርነት ልትገቡ ነው። ልባችሁ አይባባ፤ አትፍሩ፤ አትደግጡ፤ በጠላቶቻችሁ ፊት አትሸበሩ። 4 ድልን ያቀዳጃችሁ ዘንድ ስለ እናንተ ጠላቶቻችሁን ሊወጋ አብሮአችሁ የሚወጣው አምላካችሁ እግዚአብሔር ነውና። 5 አለቆቹም ለሠራዊት እንዲህ ይበሉ፥ አዲስ ቤት ሠርቶ ያላስመረቀ አለን? ወደ ቤቱ ተመልሶ ይሂድ፥ ያለበለዚያ በጦርነቱ ላይ ሲሞት፥ ቤቱን የሚያስመርቀው ሌላ ሰው ይሆናል። 6 ወይን ተክሎ ገና ያልበላለት አለን? ወደ ቤቱ ይመለስ፣ ያለበለዚያ በጦርነቱ ሲሞት፥ ሌላ ሰው ይበለዋል። 7 ሚስት አጭቶ ያላገባት አለን? ወደ ቤቱ ይመለስ፥ ያለበለዚይ በጦርነቱ ሲሞት ሌላ ሰው ያገባታል። 8 በዚያም አለቆቹ፦ የሚፈራ ወይም ልቡ የሚባባ ሰው አለን? የወንድሞችም ልብ እንዳይባባ፥ ወደ ቤቱ ይመለስ፤ በማለት ጨምረው ይናገሩ። 9 አለቆቹ ለሰራዊቱ ተናግረው ሲያበቁ አዛዦችን በሰራዊቱ ላይ ይሹሙ። 10 አንድን ከተማ ለመውጋት በምትዘምቱበት ጊዜ አስቀድማችሁ ለሕዝቧ የሰላም ጥሪ አስተላልፉ፥ 11 ከተቀበሉአችሁና ደጃቸውን ከከፊቱላችሁ በከተማዋ ውስጥ ሕዝብ ሁሉ የጉልበት ሥራ ይሥሩ፥ ያገልግላችሁም። 12 ዕርቀ ሰላምን ባለመቀበል ውጊያ ከመረጡ፥ ከተማዪቱን ክበቡአት። 13 እግዚአብሔር አምላካችሁ አሳልፎ በእጃችሁ በሰጣችሁ ጊዜ በውስጧ ያሉትን ወዶች በሙሉ በሰይፍ ግደሉአቸው። 14 ነገር ግን ሴቶቹን ሕፃናትን እንስሳትንና በከተምዩቱ ውስጥ የሚገኘውን ማናቸውንም ነገር በምርኮ ለራሳችሁ አድርጉ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ ከጠላቶቻችሁ የሚሰጣችሁን ምርኮ ልትጠቀሙበት ትችላላችሁ። 15 እንግዲህ የአካባቢያችሁ አሕዛብ ከተሞች ባልሆኑትና ከእናንተ እጅግ ርቀው በሚገኙት ከተሞች ሁሉ ላይ የምታደርጉት ይኸው ነው። 16 እግዚአብሔር አምላካችሁ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ በአሕዛብ ከተሞች ውስጥ እስትንፋስ ያለውን ነገር አታስተርፉ። 17 በዚህ ፈንታ፥ ኬጢያዊውን፥ አሞራዊውን፥ ከነዓናዊውን፥ ፌርዛዊውን፥ ኤዊያዊውን፥ ኢያቡሳዊውን እግዚአብሔር አምላካችሁ ባዘዛችሁ መሠረት ፈጽማችሁ ደምስሱአቸው። 18 አለበለዚያ አማልክታቸውን በሚያመልኩበት ጊዜ የሚፈጽሟቸውን አስጻያፊ ተግባራት ሁሉ ታደርግ ዘንድ ያስተምሩአችኋል፤ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ላይ ኃጢአት ትሠራላችሁ። 19 አንድን ከተማ ተዋገታችሁ ለመያዝ የረጅም ጊዜ ከበባ በምታድርጉበት ጊዜ፥ ዛፎቹን በመጥረቢያ ጨፍጭፋችሁ ማጥፋት የለባችሁም። የዛፎችን ፍሬ መብላት ስለምትችሉ አትቁረጡአቸው። ከባችሁ የምታጠፉአችሁ የሜዳ ዛፎች ሰዎች ናቸውን? 20 የሚበላ ፍሬ እንደማያፈራ የምታውቁትን ዛፍ ግን ልትቆርጡና ጦርነት የምታካሄዱባትን ከተማ በድል እስክትቆጣጠሩአት ድረስ ለከበባው ምሽግ መሥሪያ ልትጠቀሙበት ትችላላችሁ።



Deuteronomy 20:1

ለጦርነት በጠላቶችህ ላይ በምትወጣበት ጊዜ

“ከጠላቶችህ ጋር ለመዋጋት ወደ ጦርነት በምትወጣበት ጊዜ”

ፈረሶችን፣ ሠረገላዎችን ስታይ

ሰዎች ብዙ ፈረሶችና ሠረገላዎች ያሉትን ሰራዊት በጣም ጠንካራ እንደሆነ ይቆጥሩ ነበር። የዚህ መግለዓ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ከግብፅ ምድር ያወጣህ

እግዚአብሔር ሕዝቡን ከግብፅ ወደ ከነዓን አምጥቷቸዋል። ከግብፅ ወደ ከነዓን የሚደረገውን ጉዞ ለማመልከት “ወደ ላይ” የሚለውን ቃል የተለመደ ነበር። አ.ት፡ “ከግብፅ ምድር መርቶ ያወጣችሁ እግዚአብሔር”

Deuteronomy 20:2

ለሕዝቡ ተናገር

“ለእስራኤል ወታደሮች ተናገር”

ልባችሁ አይሸበር። አትፍሩ ወይም አትደንግጡ። አትፍሯቸው

እነዚህ አራቱም አገላለጾች ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆኑ እንዳይፈሩ ጠንከር ያለ አጽንዖት ይሰጣሉ። የአንተ ቋንቋ ይህንን አሳብ የሚገልጹ አራት መንገዶች ከሌሉት ከአራት በሚያንሱ ቃላት መጠቀም ትችላለህ። (See: Parallelism)

ልባችሁ አይሸበር

እዚህ ጋ “ልባችሁ” የሕዝቡን የሕዝቡን ድፍረት ይወክላል። የልብ መሸበር የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን “አትፍሩ” ማለት ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከጠላቶቻችሁ ጋር ለመዋጋት ከእናንተ ጋር የሚሄደው አምላካችሁ እግዚአብሔር ነው

እግዚአብሔር የእስራኤልን ጠላቶች ድል ማድረጉ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ሆኖ እንደሚዋጋ ጦረኛ ተደርጎ ተነግሮለታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሊያድናችሁ

“ድል ሊሰጣችሁ”

Deuteronomy 20:5

አለቆቹ ይናገሩ

ከአለቆቹ ሥራ አንዱ ከሰራዊቱ ማን መሰናበት እንዳለበት መወሰን ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

-- ማን አለ? ወደ ቤት ተመልሶ ይሂድ

“አዲስ ቤት ሠርቶ ያላስመረቀ ወታደር በዚህ ካለ ወደ ቤቱ ተመልሶ ይሂድ”

በጦርነት ላይ እንዳይሞትና ሌላ ሰው እንዳያስመርቀው

አለቃው አንድን ወታደር ሊያጋጥመው የሚችለውን ሁኔታ ይዘረዝራል። አ.ት፡ “እርሱ በጦርነት ላይ ቢሞት በእርሱ ፈንታ ሌላ ሰው ቤቱን እንዳያስመርቅ” (See: Hypothetical Situations)

Deuteronomy 20:6

- የተከለ አለ? ወደ ቤቱ ይሂድ

“እዚህ አዲስ ወይን ተክሎ ፍሬውን ያልሰበሰበ ወታደር ካለ ወደ ቤቱ ተመልሶ ይሂድ”

በጦርነት ላይ እንዳይሞትና ሌላ ሰው በፍሬው እንዳይደሰት

አለቃው አንድን ወታደር ሊያጋጥመው የሚችለውን ሁኔታ ይዘረዝራል። አ.ት፡ “እርሱ በጦርነት ላይ ቢሞት በእርሱ ፈንታ ሌላ ሰው ፍሬውን እንዳይሰበስብ” (See: Hypothetical Situations)

ሚስት ለማግባት ያጨ አለ? -- ወደ ቤቱ ይሂድ

“ሚስት ለማግባት ቃል ኪዳን ያደረገ፣ ነገር ግን ያላገባት የትኛውም ወታደር እዚህ ቢኖር ወደ ቤቱ ተመልሶ ይሂድ”

በጦርነት ላይ እንዳይሞትና ሌላ ሰው እንዳያገባት

አለቃው አንድን ወታደር ሊያጋጥመው የሚችለውን ሁኔታ ይዘረዝራል። አ.ት፡ “እርሱ በጦርነት ላይ ቢሞት በእርሱ ፈንታ ሌላ ሰው እንዳያገባት” (See: Hypothetical Situations)

Deuteronomy 20:8

የሚፈራና ልቡ የሚሸበርበት ሰው ማነው? ወደ ቤቱ ተመልሶ ይሂድ

“እዚህ ያለ የትኛውም ወታደር ቢፈራና ልቡ ቢሸበር ወደ ቤቱ ተመልሶ ይሂድ”

የሚፈራ ወይም ልቡ የሚሸበርበት

ሁለቱም ቃላት መሠረታዊ ትርጉማቸው አንድ ነው። አ.ት፡ “በጦርነት ለመዋጋት የሚፈራ” (See: Doublet)

እንደ ራሱ ልብ የወንድሙም ልብ እንዳይቀልጥ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እርሱ እንደፈራ ሌላውም እስራኤላዊ እንዳይፈራ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የወንድሙ ልብ -- እንደ ራሱ ልብ

እዚህ ጋ “ልብ” የሚወክለው የአንድን ሰው ድፍረት ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእነርሱ ላይ አዛዦችን ይሹሙ

“የእስራኤልን ሕዝብ እንዲመሩ አለቆቹ አዛዦችን መሾም አለባቸው”

Deuteronomy 20:10

አንድን ከተማ ለመውጋት በምትዘምትበት ጊዜ

እዚህ ጋ “ከተማ” ሕዝቡን ይወክላል። አ.ት፡ “የአንድን ከተማ ሕዝብ ለመውጋት በምትሄድበት ጊዜ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለእነዚያ ሰዎች የሰላም ጥሪ አቅርብላቸው

“በከተማው ለሚኖሩ ሰዎች እጅ እንዲሰጡ ዕድል ስጣቸው”

በሮቻቸውን ከከፈቱልህ

እዚህ ጋ “በሮች” የሚያመለክቱት የከተማይቱን በሮች ነው። “በሮቻቸውን ከከፈቱልህ” የሚለው ሐረግ የሚወክለው የሚማረኩትንና እስራኤላውያን ወደ ከተማቸው እንዲገቡ የሚፈቅዱትን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “በሰላም ወደ ከተማቸው እንድትገባ ከፈቀዱልህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 20:12

ነገር ግን ያቀረብክለትን የሰላም ጥሪ ባይቀበል

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚያመለክተው ሕዝቡን የሚወክለውን ከተማውን ነው። አ.ት፡ “ነገር ግን የከተማይቱ ሰዎች እጃቸውን ባይሰጡ” ወይም “ነገር ግን የከተማይቱ ሰዎች ያቀረብክላቸውን የሰላም ጥሪህን ባይቀበሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 20:14

ሕፃናቱን

“ልጆቹን”

ብዝበዛውን ሁሉ

“የሚጠቅሙትን ነገሮች በሙሉ”

ምርኮ

እነዚህ በጦርነት ድል ያደረጉ ሰዎች ከወጓቸው ሰዎች ላይ የሚወስዷቸው ጠቃሚ ነገሮች ናቸው።

ከተሞቹ ሁሉ

እዚህ ጋ “ከተሞች” የሚወክሉት ሕዝቡን ነው። አ.ት፡ “በከተሞች የሚኖሩት ሰዎች በሙሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 20:16

አምላክህ እግዚአብሔር ርስት አድርጎ በሚሰጥህ በእነዚህ ሰዎች ከተሞች ውስጥ

እግዚአብሔር ለሕዝቡ በከነዓን የሚሰጣቸው ከተሞች እነርሱ የሕዝቡ ርስት እንደሆኑ ተቆጥረው ተነግሮላቸዋል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እስትንፋስ ያለውን ምንም ነገር አታስቀር

“ሕይወት ያለበትን ሁሉ በሕይወት አታስቀር”። ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሕይወት ያለውን ሁሉ ግደል” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

ፈጽመህ አጥፋቸው

x

Deuteronomy 20:19

ጦርነት ዐውጅ

“በጦርነት ተዋጋ”

በመጥረቢያ ቁረጣቸው

“ዛፎቹን በመጥረቢያ ቁረጣቸው”

ልትከበው በሜዳ ላይ ያለ ዛፍ ሰው ነውን?

ይህ ሰዎቹ አስቀድመው የሚያውቁትን ለማስታወስ የቀረበ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “የፍሬ ዛፎች ሰዎች ስላልሆኑ ጠላቶችህ አይደሉም” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ለምግብነት የማይውሉ ዛፎች መሆናቸውን ስታውቅ

“የሚበላ ፍሬ የማይሰጡ ዛፎች መሆናቸውን ስታውቅ”

ከበባ ሥራባት

እነዚህ አንድን ከተማ ለመክበብ የሚያስፈልጉ መሰላሎችና ማማዎችን የመሳሰሉ መሣሪያዎችና መዋቅሮች ናቸው።

እስኪወድቅ ድረስ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “የከተማይቱ ሰዎች በጦርነቱ እስኪሸነፉ ድረስ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ይወድቃል

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚወክለው የከተማይቱን ሕዝብ የሚወክለውን ከተማ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 21

1 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንድትወርሱአት በሚሰጣችሁ ምድር ላይ አንድ ሰው ተገድሎ ሜዳ ላይ ቢገኝና ገዳዩም ማን እንደ ሆነ ባይታወቁ፥ 2 ሽማግሌዎቻችሁና ዳኞቻችሁ ወጥተው የተገደለ ሰው ሬሳው ወድቆ ከተገኘበት አንሥቶ በአቅራቢያው እስካሉት ከተሞች ድረስ ያለውን ርቀት ይለኩ። 3 ከዚያም የተገደለ ሰው ሬሳው ወድቆ ከተገኘበት ስፍራ በጣም ቅርብ የሆነችው ከተማ ሽማግሌዎች ለሥራ ያልደረሰችና ቀንበር ያልተጫነባትን ጊደር ይዘው፥ 4 ከዚያ በፊት ታርሶ ወይም ተዘርቶበት ወደማይታወቅ ወራጅ ውሃ ወዳለበት ሸለቆ ያምጡት። በዚያ ሸለቆም የጊደሪቱን አንገት ይስበሩ፥ 5 እንዲያገለግሉና በእግዚአብሔር ስም እንዲባርኩ፥ በማንኛውም የክርክርና የጥቃት ጉዳዮች ሁሉ ላይ ውሳኔ እንዲሰጡ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ መርጦአቸዋልና የሌዊ ልጆች ካህናቱ ወደ ፊት ይቅረቡ። 6 ከዚያም ሬሳው በተገኘበት አቅራቢያ ከተማ የሚኖሩ ሽማግሌዎች ሁሉ፥ በሸለቆው ውስጥ፥ አንገቷ በተሰበረው ጊደር ላይ እጃቸውን ይታጠቡ፤ 7 እንዲህም ብለው ይናገሩ፥ እጆቻችን ደም አላፈሰሱም፤ ድርጊቱ ሲፈጸምም ዐይኖቻችን አላዩም። 8 እግዚአብሔር ሆይ፥ ስለ ተቤዥኸው ሕዝብህ ስለ እስራኤል ብለህ ይህን ስርየት ተቀበል፥ ሕዝብህንም በፈሰሰው ንጹሕ ደም በደለኛ አታድርግ። ስለ ፈሰሰውም ደም ስርየት ይደረግላቸዋል። 9 በዚህም መንገድ በእግዚአብሔር ፊት ቀና የሆነውን ስታደርጉ የንጹሑን ደም የማፍሰስ በደልን ከመካከላችሁ ታስወግዳላችሁ። 10 ከጠላቶቻችሁ ጋር ጦርነት ልትገጥሙ ወጥታችሁ አምላካችሁ እግዚአብሔር እነርሱን በእጃችሁ አሳልፎ ሰጥቶአችሁ በማረካችሁ ጊዜ፥ 11 ከምርኮኞቹ መካከል ቆንጆ ሴት አይታችሁ ብትማርኩ፥ ሚስታችሁ ልታደርጉአት ትችላላችሁ፤ 12 ወደ ቤታችሁ ውሰዱአት፥ ጠጉሯን ትላጭ፥ ጥፍሯንም ትቁረጥ። 13 ስትማርኩአት የለበሰችውንም ልብስ ታውልቅ፥ እቤታችሁ ተቀምጣ ለአባትና ለናቷ ወር ሙሉ ካለቀሰችላቸው በኋላ፥ ከእርሷ ጋር ለመተኛና ባል ልትሆለት፥ እርሷም ሚስት ልትሆናችሁ ትችላለች። 14 ነገር ግን በእርሷ ደስተኛ ባትሆን፥ ወደምትፈልገው እንድትሄድ ነጻነት ስጡአት፥ ውርደት ላይ ስለ ጠላችኋት በገንዘብ ልትሸጡአት ወይም እንደ ባሪያ ልትቆጥሩአት አይገባችሁም። 15 አንድ ሰው ሁለት ሚስቶች ቢኖሩት አንደኛዋን የሚወዳት፥ ሌላዋን ግን የሚጠላት ቢሆን፥ ሁለቱም ወንዶች ልጆችን ወልደውለት፥ በኩር ልጁ ግን የተወለደው ከማይወዳት ሚስቱ ቢሆን፥ 16 ንብረቱን ለልጆቹ በሚያወርስበት ጊዜ፥ የብኩርናን መብት ከማይወዳት ሚስቱ ከወለደው በኩር ልጅ ገፎ ከሚወዳት ሚስቱ ለተወለደው ልጁ በአድልዎ መስጠት አይገባውም፤ 17 በዚህ ፈንታ፥ ከተጠላችው ሚስቱ ለተወለደው ልጅ ካለው ሁብት ሁሉ ሁለት እጥፍ ድርሻውን በመስጠት ብኩርናውን ያስታውቅ ያ ልጅ የአባቱ ኃይል መጀመሪያ ነውና የብኩርና መብት የራሱ ነው። 18 አንድ ሰው የአባቱን ወይም የእናቱን ትእዛዝ የማይሰማ፥ ቢቀጡትም የማይታረም እልከኛና ዐመፀኛ ልጅ ቢኖረው፥ 19 አባትና እናቱ ይዘው በሚኖሩበት ከተማ በር ወዳሉት አለቆች ያምጡት፥ 20 ይህ ልጃችን እልከኛና ዐመፀኛ ነው፥ አይታዘዘንም አባካኝና ሰካራም ነው ብለው ለአለቆች ይንገሯቸው። 21 ከዚያም በኋላ የከተማዪቱ ሰዎች ሁሉ እስኪሞት ድረስ በድንጋይ ይወገሩት፥ ክፉውንም ከመካከላችሁ ታስወግዳላችሁ፥ እስራኤልም ሁሉ ይህን ሰምቶ ይፈራል። 22 አንድ ሰው ለሞት የሚያበቃ በደል ፈጽሞ ቢገደልና ሬሳው በእንጨት ላይ ቢሰቀል፥ 23 ሬሳውን በእንጨት ላይ እንደ ተሰቀለ አታሳድሩት ምክንያቱም በእንጨት ላይ የተሰቀለ በእግዚአብሔር ዘንድ የተረገመ ነውና፥ አምላካችሁ እግዚአብሔር ርስት አድርጎ የሚሰጣችሁን ምድር እንዳታረክሱ በዚያኑ ዕለት ቅበሩት።



Deuteronomy 21:1

አንድ ሰው ተገድሎ ቢገኝ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ማንነቱ ባልታወቀ ሰው የተገደለን ሰው ቢያገኝ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሜዳ ላይ ወድቆ

የሞተው ሰው ሜዳ ላይ ወድቋል።

ማን እንደ ገደለው ባይታወቅ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማን እንደ ገደለው ማንም አያውቅም” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ወደ ከተሞቹ ይለኩ

“ለከተሞቹ ያለውን ርቅት ይለኩ”

የተገደለውን እርሱን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማንነቱ ያልታወቀ ሰው የገደለውን እርሱን” ወይም “ሬሳውን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 21:3

ቀንበር ያልተሸከመ

x

Deuteronomy 21:5

ወደ ፊት ይቅረቡ

“ወደ ሸለቆው ይምጡ”

አምላክህ እግዚአብሔር እርሱን እንዲያገለግሉት መርጧቸዋልና

“ካህናቱ እርሱን እንዲያገለግሉት አምላክህ እግዚአብሔር ስለመረጣቸው”

አምላካችሁ እግዚአብሔር

ሙሴ ለአንድ ሰው እንደሚናገር አድርጎ ለእስራኤል ሕዝብ ስለሚናገር “የአንተ” የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

ባርኮት እንዲሰጡ

“የእስራኤልን ሕዝብ እንዲባርኩ”

በእግዚአብሔር ስም

እዚህ ጋ “በ -- ስም” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ራሱንና የእርሱን ሥልጣን ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ራሱ የሚለውንና የሚያደርገውን የሚልና የሚያደርግ እርሱ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር እና ማንኛውንም ዓይነት ክርክርና ጥቃት በቃላቸው እንዲወስኑ

“አለመግባባቶችንና የጸብ ምክንያቶችን ሁሉ የሚፈቱት እግዚአብሔር እና እነርሱ ይሆናሉ”

Deuteronomy 21:6

አንገቷ የተሰበረን ጊደር

x

Deuteronomy 21:8

የዋጀኸውን

እግዚአብሔር በግብፅ ባሪያ የነበረውን የእስራኤልን ሕዝብ ማዳኑ ሕዝቡን ከባርነት ለመቤዠት ገንዘብ እንደከፈለላቸው በሚመስል መልኩ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በንጹሕ ደም ምክንያት በሕዝብህ በእስራኤል መካከል በደልን አታኑር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ሕዝብ ንጹሕን ሰው እንደ ገደሉ በደለኞች አድርገህ አትቁጠራቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም ስለ ፈሰሰው ደም ይቅር ይባላሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከዚያም ስለ ንጹሑ ሰው ሞት እግዚአብሔር ሕዝቡን እስራኤልን ይቅር ይላቸዋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕን ደም ከመካከልህ ታስወግዳለህ

“ንጹሕን ሰው ስለ መግደልህ ከእንግዲህ በደለኛ አትሆንም”

በእግዚአብሔር ዐይን ትክክል የሆነውን

x

Deuteronomy 21:10

ውጣ

“እናንተ ወታደሮች የሆንችሁ ውጡ”

ብትመኛት

“ከእርሷ ጋር ለመተኛት ብትፈልግ” ለሚለው የትህትናን ሐረግ ተጠቀም።

ሚስትህ እንድትሆን ልትወስዳት ብትፈልግ

“ለታገባት ብትፈልግ”

ጸጉሯን ትላጨው

“ጸጉሯን ከራሷ ላይ ትመለጠው”

ጥፍሮቿን ትቆረጥ

“የጣቶቿን ጥፍር ትቁረጥ”

Deuteronomy 21:13

የለበሰችውን ልብስ ታውልቀው

ይህንን የምታደርገው በዘዳግም 21፡12 እንደተጠቀሰው ሰውየው ወደ ቤቱ ካመጣትና ጸጉሯን ተቆርጣ፣ የእጅና የእግር ጣት ጥፍሮቿን ከተቆረጠች በኋላ ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የሕዝቧን ልብስ ታወልቅና የእስራኤላውያንን ልብስ ትለብሳለች” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ተማርካ በተወሰደች ጊዜ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እርሷን በማረክህ ጊዜ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

አንድ ሙሉ ወር

“ወሩን በሙሉ” ወይም “አንድ ወር ሙሉ”

ነገር ግን ባትደሰትባት

ሰውየው ከሴቲቱ ጋር ስለ መተኛቱ ግልጽ ማድረግ ያስፈልግህ ይሆናል። አአ.ት፡ “ነገር ግን አብረሃት ከተኛህ በኋላ ሚስትህ እንዳትሆን ከወሰንክ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ወደፈለገችበት ትሂድ

“መሄድ ወደምትፈልግበት ትሂድ”

አዋርደሃታልና

“ከእርሷ ጋር ከተኛህ በኋላ ስለ ሰደድካት አሳፍረሃታልና”

Deuteronomy 21:15

አንዷ የተወደደችና ሌላይቱ የተጠላች

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች፣ 1) “ሰውየው ከሚስቶቹ አንደኛዋን ይወዳል፣ ሌላይቱን ሚስቱን ይተላታል” ወይም 2) “ሰውየው ሌላይቱን ሚስቱን ከሚወድበት በበለጠ አንደኛውን ሚስቱን ይወዳታል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሁለቱም ልጆችን ቢወልዱለት

“ሁለቱም ሚስቶቹ ልጆችን ወልደውለታል”

በኩሩ ከተጠላችው ከሆነ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በኩሩ ሰውየው ከሚጠላት ሚስቱ የተወለደ ከሆነ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም ሰውየው በ-- ቀን

“ሰውየው በ-- ጊዜ”

ሰውየው ያለውን ልጆቹ እንዲወርሱ ያደርጋል

“ሰውየው ንብረቱን ለልጆቹ ርስት አድርጎ ይሰጣቸዋል”

ከተወደደች ሚስቱ የተወለደውን ልጅ ከተጠላችው ሚስቱ በተወለደው ልጅ ፊት በኩር አያድርገው

“ከተጠላችው ሚስቱ በተወለደው ልጅ ምትክ ከተወዳጅ ሚስቱ የተወለደውን ልጅ በኩር አያድርገው”

ዕጥፍ ድርሻ

“ሁለት ዕጥፍ”

ያ ልጅ የጉብዝናው ጅምሬ ነው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ያ ልጅ ሰውየው የወንዶች ልጆች አባት መሆኑን የሚያሳይ ነው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 21:18

የአባቱን ቃል ወይም የእናቱን ቃል የማይታዘዝ

እዚህ ጋ “ድምፅ” አንድ ሰው የሚናገረውን የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “አባቱ ወይም እናቱ የሚሉትን የማይታዘዝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ያርሙት

“ስለ መጥፎ ተግባሩ ይቅጡት” ወይም “ያሰልጥኑትና ያስተምሩት”

ይዘው ያምጡት

“እንዲመጣ ያስገድዱት”

Deuteronomy 21:20

ይህ የእኛ ልጅ

“ልጃችን”

ድምፃችንን አይታዘዝም

እዚህ ጋ “ድምፅ” አንድ ሰው የሚናገረውን የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ወይም የሙሉው ሰው ተምሳሌት ነው። አ.ት፡ “እንዲያደርግ የምንነግረውን አያደርግም” ወይም “አይታዘዘንም” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Synecdoche የሚለውን ተመልከት)

ሆዳም

ብዙ የሚበላና የሚጠጣ ሰው

ሰካራም

አስካሪ መጠጥ አብዝቶ የሚጠጣና ብዙ ጊዜ የሚሰክር ሰው

እስኪሞት ድረስ በድንጋይ ውገሩት

“እስኪሞት ድረስ ድንጋይ ወርውሩበት”

ክፉን ከመካከልህ ታርቃለህ

ቅጽሉ “ክፉ” ስማዊ ሐረግ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ይህንን ክፉ ነገር የሚያደርገውን ሰው ከእስራኤላውያን መካከል ታርቃለህ” ወይም “ይህንን ክፉ ሰው ግደለው” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

እስራኤል ሁሉ

“እስራኤል” የሚለው ቃል የእስራኤልን ሕዝብ የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስለ እርሱ ሰምተው ይፈራሉ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በልጁ ላይ ስለሆነው ነገር ይሰማሉ፣ እነርሱንም ሕዝቡ እንዳይቀጣቸው ይፈራሉ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 21:22

አንድ ሰው ሞት የሚገባውን ኃጢአት ሠርቶ ከሆነ

“አንድ ሰው በሞት ልትቀጣው እስከሚያስፈልግህ ድረስ እጅግ የከፋ ነገር ካደረገ”

ይገደል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አስወግደው” ወይም “ግደለው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በዛፍ ላይ ስቀለው

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) “ከሞተ በኋላ ዛፍ ላይ ስቀለው” ወይም 2) “ግደለውና በቋሚ እንጨት ላይ ስቀለው”

በዚያው ቀን ቅበረው

“በምታስወግደው ጊዜ በዚያው ቀን ቅበረው”

የተሰቀለ ሁሉ በእግዚአብሔር የተረገመ ነው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) “ሰዎች የሚሰቅሉትን ሁሉ እግዚአብሔር ይረግማቸዋል” እና 2) “ሰዎች እግዚአብሔር የረገማቸውን በዛፍ ላይ ይስቀሏቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ምድሪቱን አታርክስ

እግዚአብሔር የረገመውን በዛፍ ላይ ሰቅለህ በመተው


Chapter 22

1 የእስራኤላዊ ወንድማችሁ በሬ ወይም በግ ጠፍቶ ሲባዝን ብታዩ ወደ እርሱ መልሳችሁ አምጡለት እንጂ ዝም ብላችሁ አትለፉት፥ 2 ወንድማችሁ በአቅራቢያ ባይኖር፥ ወይም የማን መሆኑን የማታውቁ ከሆነ ባለቤቱ ፈልጎ እስኪ መጣ ድረስ ወደ ቤታችሁና ወስዳችሁ ከእናንተ ዘንድ አቆዩት፤ ከዚያም መልሳችሁ ስጡት። 3 የእስራኤላዊ ወንድማችሁን አህያ ወይም ልብስ ወይም የጠፋበትን ማናቸውንም ነገር ስታገኙ እንደዚህ አድርጉ፥ በቸልታ አትለፉት። 4 የወንድማሁ አህያ ወይም በሬ መንገድ ላይ ወድቆ ብታዩት በእግሩ እንዲቆም ርዳው እንጂ አልፋችሁ አትሂዱ። 5 ሴት የወንድ ልብስ አትልበስ፤ ወንድም የሴት ልብስ አይልበስ፤ እንዲህ የሚያደርገውን ሁሉ እግዚአብሔር አምላካችሁ ይጸየፈዋልና። 6 በመንገድ ስታልፉ አንዲት ወፍ ጫጩቶቿን ወይም ዕንቁላሎቿን የታቀፈችበትን ጎጆ በዛፍ ወይም በመሬት ላይ ብታገኙም እናቲቱን ከነጫጩቶቿ አትውሰፉ፤ 7 ጫጩቶቿን መውሰድ ትችላላችሁ እናቲቱን ግን መልካም እንዲህንላችሁና ዕድሜአችሁም እንዲርዝም ልቀቁት፤ 8 አዲስ ቤት በምትሠሩበት ጊዜ፥ ከጣራው ላይ ሰው ወድቆ ቤታችሁ ላይ የደም በደል እንዳታመጡ፥ በጣራው ዙሪያ መከታ አብጁለት። 9 በወይን ተክል ቦታችሁ ውስጥ ሁለት ዓይነት ዘር አትዝሩ ይህን ካደረጋችሁም የዘራችሁት ሰብል ብቻ ሳይሆን የወይን ፍሬአችሁ ይጠፋል። 10 በሬና አህያ በአንድ ላይ ጠምዳችሁ አትረሱ። 11 ሱፍና ሐር አንድ ላይ ተፈትሎ የተሠራ ልብስ አትልበሱ። 12 በምትለብሱት ልብስ ላይ በአራቱ ማእዘኖች ዘርፍ አድርጉ። 13 አንድ ወንድ ሚስት አግብቶ አብሮአት ከተኛ በኋላ ቢጠላት፥ 14 ስሟንም በማጥፋት፥ ይህችን ሴት አገባኋት፥ዳሩ ግን በደረስሁባት ጊዜ ድንግልናዋን አላገኘሁም ቢል፥ 15 የልጂቱ አባትና እናት ድንግልናዋን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ይዘው በከተማዪቱ በር ወዳሉት አለቆች ይምጡ። 16 የልጂቱም አባት ለአለቆቹ እንዲህ ይበል፥ ልጄን ለዚህ ሰው ዳርሁለት፥ እርሱ ግን ጠላት፤ 17 ስሟንም በማጥፋት ልጅህን ከነድንግልናዋ አላገኘኋትም ብሎኛል፤ ነገር ግን የልጄ ድንግልና ማረጋገጫ ይኸውላችሁ። ከዚያም ወላጆቿ የደሙን ሸማ በከተማዪቱ አለቆች ፊት ይዘርጉት። 18 ከዚያም በኋላ አለቆቹ ሰውየውን ይዘው ይቅጡት፥ 19 ይህ ሰው የአንዲት እስራኤላዊት ድንግል ስም አጥፍቶአልና አንድ መቶ ሰቅል ብር ያስከፍሉት፥ ገንዘቡንም ለልጂቱ አባት ይስጡት፥ ሴቲቱም ሚስቱ ሆና ትኖራለች፤ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሊፈታት አይችልም። 20 ሆኖም ክሱ እውነት ሆኖ ሴቲቱ ድንግል ለመሆኗ ምንም ማረጋገጫ ማቅረብ ካልተቻለ፥ 21 በአባቷ ቤት ሳለች በማመንዘር በእስራኤል ውስጥ አሳፋሪ ተግባር ፈጽማለችና ወደ አባቷ ቤት ደጃፍ ያምጣት፥ እዚያም የከተማዋ ሰዎች እስክትሞት ድረስ በድንጋይ ይውገሯት። 22 አንድ ሰው ከሌላ ሰው ሚስት ጋር ተኝቶ ቢገኝ፥ አብሮአት የተኛው ሰውና ሴቲቱ ሁለቱም ይገደሉ። ክፉውን ከእስራኤል ማስወገድ አለባችሁ። 23 አንድ ሰው የታጨች ድንግል በከተማ ውስጥ አግኝቶ ከእርሷ ጋር ቢተኛ፥ ልጃገረዲቱ በከተማ ውስጥ እያለች አስጥሉኝ ብላ ስላልጮኸች፥ ሰውየውም የሌላን ሰው ሚስት አስግድዶ ስለ ደፈረ፥ 24 ሁለቱንም ወደ ከተማ ደጃፍ ወስዳችሁ እስኪሞቱ ድረስ በድንጋይ ውገሯቸው። ክፉውን ከመካከላችሁ ማስወገድ አለባችሁ። 25 ነገር ግን አንድ ሰው የታጨችውን ልጃገረድ ከከተማ ውጭ አግኝቶ በማስገደድ ቢደፍራት፥ ይህን ድርጊት የፈጸመው ሰው ብቻ ይገደል። 26 በልጃገረዲቱ ላይ ግን ምንም አታድርጉባት፥ ለሞት የሚያበቃ ኃጢአት ምንም አልሠራችም፥ ይህ ዓይነቱ ጉዳይ አደጋ ጥሎ ባልንጀራውን ከሚገድል ሰው አድራጎት ጋር የሚመሳሰል ነው። 27 ምክንያቱም ሰውየው የታጨችውን ልጃገረድ ከተማ ውጭ ስላገኛትና ብትጮኽም እንኳ ለርዳታ የደረሰላት ምንም ሰው ስላልነበር ነው። 28 አንድ ሰው ያልታጨች ልጃገረድ አግኝቶ በማስገደድ ቢደርስባትና ቢጋለጡ 29 ሰውየው ለልጅቷ አባት አምሳ ስቅል ብር ይክፈል፥ ልጃገረዲቱን አስገድዶ ደፍሮአታልና እርሷን ማግባት አለበት፥ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሊፈታት አይችልም። 30 አንድ ሰው አባቱን ሚስት ማግባት የለበትም፥ የአባቱንም መኝታ አያርክስ።



Deuteronomy 22:1

ሲጠፋ

“ከባለቤቱ ርቆ ሲሄድ”

ራስህን ከእነርሱ አትደብቅ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንዳላየኻቸው አትሁን” ወይም “ምንም ነገር ሳታደርግ አትሂድ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እስራኤላዊ ወንድምህ በአቅራቢያህ ባይኖር

“እስራኤላዊ ወንድምህ ከአንተ ርቆ የሚኖር ከሆነ”

ወይም የማታውቀው ከሆነ

“ወይም የእንስሳው ባለቤት ማን እንደሆነ ካላወቅህ”

እርሱ እስኪፈልገው ድረስ በአንተ ዘንድ ይቆይ

“ባለቤቱ ፈልጎት እስኪመጣ ድረስ እንስሳው በአንተ ዘንድ ይቆይ”

Deuteronomy 22:3

በአህያውም ላይ እንደዚሁ አድርግ

“አህያውንም በተመሳሳይ መንገድ መልስለት”

በልብሱም ላይ እንደዚሁ አድርግ

“በተመሳሳይ መንገድ ልብሱን መልስለት”

Deuteronomy 22:5

ለወንድ የሚገባውን

“የወንድ ልብስ”

Deuteronomy 22:6

የወፍ ጎጆ

ወፎች ከጭራሮ፣ ሣር፣ እጽዋትና ጭቃ ለራሳቸው የሚሠሩት ቤት

ከጫጩቶቿ ወይም በውስጧ ካሉ ዕንቁላሎች ጋር

“ከትናንሽ ወፎች ወይም በጎጆው ውስጥ ካሉ ዕንቁላሎች ጋር”

በትናንሾቹ ላይ የተቀመጠች እናት

“እናቲቱ ወፍ በጫጩት ወፎች ላይ ተቀምጣለት”

ቀኖችህ እንዲረዝሙ

ረጅም ቀናት የረጅም ዕድሜ ዘይቤአዊ አነጋገሮች ናቸው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ረጅም ዓመት መኖር እንድትችል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:9

ምርትህ በሙሉ በተቀደሰው ስፍራ እንዳይወረስ

“ቅዱስ ስፍራ” የሚለው ቃል በተቀደው ስፍራ የሚሠሩትን ካህናት የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ቅዱስ ስፍራ ያሉ ካህናት ምርቱን ሁሉ እንዳይወስዱት” ወይም “ምርቱን ሁሉ እንዳታረክሰውና ካህናቱ ከመጠቀም እንዳይከለክሉህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በወይን ተክል ቦታ የሚበቅለውን

“በወይን ተክል ቦታ የሚበቅለውን ፍሬ”

ሱፍ

በበጎች ላይ የሚበቅል ለስላሳና የሚጠቀለል ጸጉር

በፍታ

ከቃጫ ተክል የሚሠራ ክር (የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:12

ጥለት

በአንድ ላይ ታስረው በእያንዳንዱ የካባው ማዕዘን ላይ የሚንጠለጠሉ ክሮች

ካባ

አንድ ሰው በሌሎች ልብሶቹ ላይ ደርቦ የሚለብሰው ረዘም ያለ ልብስ

Deuteronomy 22:13

ከዚያም አሳፋሪ ስለሆነ ነገር ቢከሳት

“ከዚያም ከጋብቻዋ በፊት ከሌላ ሰው ጋር ስለመተኛቷ ቢከሳት”

ምስክርነቷን ያበላሻል

የነገር ስም የሆነው “ምስክርነት” እንደ ግሥ ሐረግ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ሰዎች መጥፎ ሰው እንደሆነች እንዲያስቡ ያደርጋል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:15

የድንግልናዋን ማረጋገጫ ይውሰዱ

የነገር ስም የሆኑት “ማረጋገጥ” እና “ድንግልና” እንደ ግሣዊ ሐረጎች ሊተረጎሙ ይችላሉ። አ.ት፡ “ቀደም ሲል የግብረ ሥጋ ግንኙነት እንዳልነበራት የሚያረጋግጥ አንዳች ነገር ውሰድ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:16

ስለ አሳፋሪ ነገር ከሷታል

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ሳያገባት በፊት ከሌላ ሰው ጋር ስለመተኛቷ ከሷታል” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ከልጅህ የድንግልና ማረጋገጫ አላገኘሁኝም

የነገር ስም የሆኑት “ማረጋገጥ” እና “ድንግልና” እንደ ግሣዊ ሐረጎች ሊተረጎሙ ይችላሉ። አ.ት፡ “ልጅህ ቀደም ሲል የግብረ ሥጋ ግንኙነት ላለመፈጸሟ ማረጋገጫ ማቅረብ አልቻለችም” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ነገር ግን የልጄ ድንግልና ማስረጃው ይኸው

የነገር ስም የሆኑት “ማረጋገጥ” እና “ድንግልና” እንደ ግሣዊ ሐረጎች ሊተረጎሙ ይችላሉ። አ.ት፡ “ይሁን እንጂ ልጄ ቀደም ሲል የግብረ ሥጋ ግንኙነት እንዳልፈጸመች ይህ ያረጋግጣል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም በከተማይቱ ሽማግሌዎች ፊት ጨርቁን ይዘረጉታል

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከዚያም ድንግል እንደነበረች ማስረጃ እንዲሆን እናትና አባቷ በደም የተነከረውን ጨርቅ ለሽማግሌዎቹ ያሳያሉ።(See: Assumed Knowledge and Implicit Information

Deuteronomy 22:18

ይቅጡት

“ቅጣት እንዲከፍል ያድርጉት”

አንድ መቶ ሰቅል

“100 ሰቅል” (ገንዘብ በመጽሐፍ ቅዱስ እና ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ለልጅቱ አባት ይስጡት

“ገንዘቡን ለልጅቱ አባት ስጡት”

የእስራኤል ድንግል ምስክርነቷ እንዲበላሽ አድርጓል

የነገር ስም የሆነው “ምስክርነት” እንደ ግሣዊ ሐረግ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ሰዎች የእስራኤልን ድንግል መጥፎ ሰው አድርገው እንዲያስቧት አድርጓል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

እንዳይሰዳት

“እንዲፈታት በፍጹም አትፍቀድለት”

በቀኖቹ ሁሉ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ሕይወቱን ሙሉ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:20

ሆኖም ይህ ነገር እውነት ቢሆን

“ሆኖም እውነት ቢሆን” ወይም “ሆኖም ሰውየው የተናገረው እውነት ቢሆን”

በልጅቱ ላይ የድንግልና ማስረጃ ባይገኝ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሰውየው ልጅቱ ድንግል ስለመሆኗ ማረጋገጫ አላገኘም” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የድንግልና ማረጋገጫ

የነገር ስም የሆኑት “ማረጋገጫ” እና “ድንግልና” እንደ ግሣዊ ሐረጎች ሊተረጎሙ ይችላሉ። አ.ት፡ “ልጅቱ የግብረ ሥጋ ግንኙነት ፈጽማ እንደማታውቅ የሚያስረዳ አንዳች ነገር” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም ልጅቱን ያውጧት

“ከዚያም ሽማግሌዎቹ ልጅቱን ያውጧት”

በድንጋይ ወግረው ይግደሏት

“እስክትሞት ድረስ ድንጋይ ወርውሩባት”

በእስራኤል ውስጥ አሳፋሪ ተግባር ፈጽማለችና

“በእስራኤል ውስጥ አሳፋሪ ነገር አድርጋለችና”

በአባቷ ቤት ውስጥ እንደ ሴተኛ አዳሪ ለማድረግ

“በአባቷ ቤት ውስጥ እየኖረች እንደ ሴተኛ አዳሪ ማድረግ”

ክፉን አስወግድ

ቅጽል የሆነው “ክፉ” እንደ ስማዊ ሐረግ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ይህንን ክፉ ነገር ያደረገውን ከእስራኤላውያን መካከል አስወግድ” ወይም “ይህንን ክፉ ሰው አስወግደው” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:22

አንድ ሰው --- ቢገኝ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ሌላውን ሰው ቢያገኝ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ታስወግዳለህ

“በዚህ መንገድ ታስወግዳለህ”

Deuteronomy 22:23

ለአንድ ሰው የታጨች

“አንድን ሰው እንድታገባ ቃል የተገባላት”

ውሰዱ -- እና ውገሩ

እነዚህ ትዕዛዛት ለእስራኤል እንደ ቡድን የተነገሩ ናቸው፣ በመሆኑም ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

ሁለቱንም ውሰዷቸው

“ከዚያም ልጅቱንና ከእርሷ ጋር የተኛውን ሰው አምጧቸው”

ምክንያቱም አልጮኸችም

“ምክንያቱም ለእርዳታ አልተጣራችም”

የባልንጀራውን ሚስት አርክሷልና

በዚያን ዘመን እስራኤላውያን ለጋብቻ የተጫጩ ወንድና ሴትን እንደ ባልና ሚስት ይቆጥሯቸው ነበር። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ምክንያቱም የእስራኤላዊ ወንድሙ ከምትሆን ልጅ ጋር ተኝቷል” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ክፉን ከመካከልህ አስወግድ

ቅጽሉ “ክፉ” እንደ ስማዊ ሐረግ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ይህንን ክፉ ነገር ያደረገውን ሰው ከእስራኤላውያን መካከል አስወግደው” ወይም “ይህንን ክፉ ሰው አስወግደው” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:25

የታጨችውን ልጅ

ይህ ማለት ወላጆቿ አንድን ሰው እንድታገባ የተስማሙባት፣ ሆኖም ገና ያላገባችው ልጅ ማለት ነው።

ከዚያም ከእርሷ ጋር የተኛው ሰው ብቻ ይገደል

“ከዚያም ከእርሷ ጋር የተኛውን ሰው ብቻ ግደሉ”

ልጅቱ ጋ ለሞት የሚያበቃት ኃጢአት የለም

“ስላደረገችው ነገር በሞት አትቅጧት”

ይህ ጉዳይ ባልንጀራውን ከሚያጠቃና ከሚገድለው ሰው ጋር ተመሳሳይ ነውና

“ምክንያቱም ይህ ሁኔታ አንድ ሰው ሌላውን ሰው አጥቅቶ ከሚገድልበት ሁኔታ ጋር ስለሚመሳሰል ነው”

ከሰፈር ውጪ አግኝቷታልና

“ምክንያቱም ሰውየው ልጅቱን ከሰፈር ውጪ ሥራ ላይ ሆና አግቷታል”

Deuteronomy 22:28

ሆኖም ያልታጨች

“ሆኖም ወላጆቿ ለሚያገባት ሰው እንደሚድሩለት ቃል ያልገቡለት”

ቢገኙ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ስለሆነው ነገር ቢያውቅ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሃምሳ ሰቅል ጥሬ ብር

አንድ ሰቅል አሥራ አንድ ግራም ይመዝናል። አ.ት፡ “አምሳ የጥሬ ብር ዝርዝር” ወይም “550 ግራም ጥሬ ብር” (See: Biblical Money and Numbers)

በቀኖቹ ሁሉ አይስደዳት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ዕድሜውን ሙሉ አይፍታት” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 22:30

የአባቱን ሚስት ለራሱ ሚስት አድርጎ አይውሰድ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ምንም እንኳን እናቱ ባትሆንም የቀድሞ የአባቱን ሚስት ማግባት የለበትም” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)


Chapter 23

1 ብልቱ የተቀጠቀጠ ወይም የተቆረጠ ማናቸውም ሰው ወደ እግዚአብሔር ጉባኤ አይግባ። 2 ዲቃላም ይሁን፥ የዲቃላው ዘር የሆነ ሁሉ እስከ አሥር ትውልድ ድረስ እንኳን ቢሆን ወደ እግዚአብሔር ጉባኤ አይግባ። 3 አሞናዊም ሆነ ሞዓባዊ ወይም ማናቸውም የእርሱ ዘር፥ እስከ አሥር ትውልድ እንኳ ቢሆን ወደ እግዚአብሔር ጉባኤ አይግባ። 4 ምክንያቱም ከግብፅ ከወጣችሁ በኋላ በጉዞ ላይ በነበራችሁበት ጊዜ እህልና ውሃ ይዘው አልተቀበሏችሁም። በመስጴጦምያ በምትገኘው በፐቶር ይኖር የነበረውን የቢዖርን ልጅ በለዓምም እናንተን እንዲረግም በገንዘብ ገዙት። 5 ነገር ግን እግዚአብሔር አምላካችሁ በብዓምን አልሰማውም፤ አምላካችሁ እግዚአብሔር ስለሚወዳችሁ ርግማኑን ወደ በረከት አደረገላችሁ። 6 በሕይወት ዘመናችሁ ሁሉ ሰላምን ለእነርሱ አትመኙ። 7 ወንድማችሁ ስለ ሆነ ኤዶማዊውን አትጸየፈው፤ መጻተኛ ሆናችሁ በአገሩ ኖራችኋልና ግብፃዊውን አትጥሉት። 8 ለእነርሱ የተወለዳቸው የሦስተኛው ትውልድ ልጆች ወደ እግዚአብሔር ጉባኤ መግባት ይችላሉ። 9 ጠላታችሁን ለመውጋት ወጥታችሁ በሰፈራችሁ ጊዜ ከማናቸውም ርኩሰት ራሳችሁን ጠብቁ። 10 ከመካከላችሁ ሌሊት ዘር በማፍሰስ የረከስሰው ቢኖር፥ ከሰፈር ወጥቶ እዚያው ይቆይ። 11 እየመሸ ሲመጣ ግን ገላውን ይታጠብ ፀሐይ ስትጠልቅም ወደ ሰፈሩ ይመለስ። 12 ለመጸዳጃ የሚሆንህን ቦታ ከሰፈር ውጭ አዘጋጅ። ከትጥቅህም ጋር መቆፍሪያ ያዝ፥ 13 በምትጸዳዳበት ጊዜ አፈር ቆፍረህ በዐይነ ምድርህ ላይ መልስበት። 14 እግዚአብሔር አምላክህ ሊጠብቅህ ጠላቶህንም በእጅህ አሳልፎ ሊሰጥህ በሰፈር ውስጥ ስለሚዘዋወር በመካከልህ አንዳች ነውር አይቶ ከአንተ እንዳይመለስ፥ ሰፈርህ የተቀደሰ ይሁን። 15 አንድ ባሪያ ከአሳዳሪው ኮብልሎ ወደ እናንተ ቢመጣ፥ 16 ለአሳዳሪው አሳልፋችሁ አትስጡት፥ ደስ በሚያሰኘው ቦታን ራሱ በመረጠው ከተማ በመካከላችሁ ይኑር፤ እናንተም አታስጨንቁት። 17 ወንድ ወይም ሴት እስራኤላዊ የቤተ ጣዖት አመንዝራ አይኑራችሁ። 18 ለዝሙት አዳሪ ሴት ወይም ለወንድ ዝሙተኛ የተከፈለውን ዋጋ ለማናቸውም ስእለት አድርጋችሁ ለመስጠት ወደ እግዚአብሔር ወደ አምላካችሁ ቤት አታምጡ፤ እግዚአብሔር አምላካችሁ ሁለቱንም ይጸየፋቸዋልና። 19 የገንዘብ፥ የእህል ወይም የማንኛውንም ነገር ወለድ ለማግኘት ለወንድማችሁ በወለድ አታበድሩ። ባዕድ ለሆነ ሰው በወለድ ማበደር ትችላላችሁ። 20 ነገር ግን ልትወርሱአት በምትገቡባት ምድር እጃችሁ በሚነካው በማናቸውም ነገር እግዚአብሔር አምላካችሁ እንዲባርካችሁ ለእስራኤልዊ ወንድማችሁ በወለድ አታበድሩት። 21 ለእግዚአብሔር ለአምልካችሁ ስእለት ከተሳላችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ አጥብቆ ከእናንተ ይሻዋልና፤ ኃጢአት እንዳይሆንባችሁ ለመክፈል አትዘግዩ። 22 ሳትሳሉ ብትቀሩ ግን በደለኛ አትሆኑም። በአንደበታችሁ የተናገራችሁትን ሁሉ ለመፈጸም ጠንቃቃ ሁኑ፥ 23 ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር በገዛ አንደበታችሁ ፈቅዳችሁ ስእለት ተስላችኋልና። 24 ወደ ባልንጀራችሁ የወይን ተክል ቦታ በምትገቡበት ጊዜ ያሰኛችሁን ያህል መብላት ትችላላችሁ፤ ነገር ግን አንዳችም በዕቃችሁ አትያዙ። 25 ወደ ባልንጀራችሁ እርሻ በምትገቡበት ጊዜ እሸት መቅጠፍ ትችላላችሁ፤ በሰብሉ ላይ ግን ማጭድ አታሳርፉበት።



Deuteronomy 23:1

ተቀጥቅጦ የቆሰለ ወይም የተቆረጠ ሰው

“የወንድ አካሉ የተቀጠቀጠ ወይም የተቆረጠበት ሰው”

ወደ እግዚአብሔር ጉባዔ መግባት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ማኅበረሰብ ሙሉ አባል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ዲቃላ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ወላጆቹ ዘመዳሞች ሆነው ወይም በዝሙት የወለዱት ልጅ ወይም 2) ከሴተኛ አዳሪ የተወለደ ልጅ።

ተወላጆቹ እስከ አሥረኛ ትውልድ ድረስ

ይህ “አሥረኛ” የአሥር ደረጃን አመልካች ቁጥር ነው። አ.ት፡ “ከዲቃላው ልጅ ተወላጆች አሥረኛ ትውልድ በኋላ እንኳን” (ደረጃን አመልካች ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

ማናቸውም

“ከእነዚህ ተወላጆች ማናቸውም”

Deuteronomy 23:3

ወደ እግዚአብሔር ጉባዔ አይግቡ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ማኅበረሰብ ሙሉ አባል አይሁኑ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ተወላጆቹ እስከ አሥረኛ ትውልድ ድረስ

ይህ “አሥረኛ” የአሥር ደረጃን አመልካች ቁጥር ነው። አ.ት፡ “ከተወላጆቹ ከአሥር ትውልድ በኋላ እንኳን” (ደረጃን አመልካች ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

በእንጀራና በውሃ አልተቀበሏችሁም

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ምግብና መጠጥ በማቅረብ አልተቀበሏችሁም” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

በአንተ ላይ -- እንዲረግማችሁ

ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚለው ቃል እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

Deuteronomy 23:5

አልሰማም

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ትኩረት አልሰጠውም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እርግማኑን ወደ በረከት ለወጠልህ

“እንዲረግምህ ሳይሆን እንዲባርክህ አደረገው”

ሰላማቸውን ወይም ብልጽግናቸውን በፍጹም አትፈልግ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፣ 1) “ከአሞናውያንና ከሞዓባውያን ጋር የሰላም ስምምነት ከቶ ማድረግ የለብህም” ወይም 2) “ለእነዚያ 2 የሕዝብ ወገኖች መልካም እንዲሆንላቸውና ለመበልጸግ የሚያስችላቸውን ምንም ነገር አታድርግ”

በቀኖችህ ሁሉ

x

Deuteronomy 23:7

ኤዶማዊውን አትጸየፈው

“ኤዶማዊውን አትጥላው”

ወንድምህ ነውና

“ዘመድህ ነውና”

ግብፃዊውን አትጸየፈው

“ግብፃዊውን አትጥላው”

የሚወለዱላቸው የተወላጆቻቸው ሦስተኛ ትውልድ ወደ እግዚአብሔር ጉባዔ እንዲገቡ

ይህ “ሦስተኛ” የሦስት ደረጃን አመልካች ቁጥር ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ኤዶማዊ ወይም ግብፃዊ በእስራኤላውያን ማኅበረሰብ ውስጥ ለመኖር ቢመጣ፣ የልጅ ልጆቹ የዚያ ማኅበረሰብ ሙሉ አባል ሊሆኑ ይችላሉ” (See: (ደረጃን አመልካች ቁጥር እና Assumed Knowledge and Implicit Information የሚለውን ተመልከት))

Deuteronomy 23:9

እንደ ሰራዊት በጠላቶችህ ላይ በምትወጣበት ጊዜ፣ ያን ጊዜ ራስህን ጠብቅ

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

በጠላቶችህ ላይ

“ጠላቶችህን ለመውጋት”

ከክፉ ነገር ሁሉ ራስህን ጠብቅ

“መጥፎ ከሆኑ ነገሮች ሁሉ ራስህን አርቅ”

ሌሊት በሆነበት ነገር ምክንያት ንጹሕ ያልሆነ ማንኛውም ሰው

ይህ ዘር ማፍሰሱ የተነገረበት የትህትና አባባል ነው። አ.ት፡ “በእንቅልፍ ላይ እያለ ዘር ስለፈሰሰው ንጹሕ ያልሆነ ማንኛውም ሰው” (See: Euphemism)

Deuteronomy 23:12

የምትቆፍርበት መሣሪያ ይኑርህ

“ለመቆፈር የምትጠቀምበት መሣሪያ ይኑርህ”

Deuteronomy 23:15

ከጌታው ያመለጠ ባሪያ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከሌላ ሀገር ከጌታው አምልጦ ወደ እስራኤል የመጣ ባሪያ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ከአንተ ጋር ይኑር

“ባሪያው በሕዝብህ መካከል ይኑር”

Deuteronomy 23:17

የቤተ ጣዖት አመንዝራ -- የቤተ ጣዖት አመንዝራ -- ዝሙት አዳሪ -- ውሻ

እግዚአብሔር በማንኛውም ሰው በየትኛውም ምክንያት በወንድና በሴት የሚደረጉ የአመንዝራነት ዓይነቶችን የሚከለክል ዝርዝር ይሰጣቸዋል። (See: Merism)

በሴቶች ልጆች መካከል -- በወንዶች ልጆች መካከል -- የቤተ ጣዖት አመንዝራ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፤ ሙሴ፣ 1) ሴቶችና ወንዶች ወሲባዊ ተግባርን የመቅደስ አገልግሎት አካል እንዳያደርጉ ይከለክላቸዋል ወይም 2) ሴቶችና ወንዶች ገንዘብ ለማግኘት ወሲባዊ ተግባር እንዳይፈጽሙ ለመከልከል ሻል ባለ ቃል ይጠቀማል። (See: Euphemism)

የዝሙት አዳሪን ዋጋ ወደ -- ቤት አታምጣ

“በዝሙት ሥራ ገንዘብ የምታገኝ ሴት ያንን ገንዘብ ወደ -- ቤት አታምጣ”

ውሻ

ገንዘብ ለማግኘት ከእርሱ ጋር ወንዶች ወሲብ እንዲፈጽሙ የሚፈቅድ ወንድ

ወደ አምላክህ ወደ እግዚአብሔር ቤት

“ወደ መቅደስ”

ለየትኛውም ስእለት

“ስእለት ለመፈጸም”

እነዚህን በሙሉ

የሴትና የወንድ ዝሙት አዳሪዎችን ዋጋ

Deuteronomy 23:19

ለእስራኤላዊ ወንድምህ በወለድ አታበድረው

“ለእስራኤላዊ ወንድምህ አንዳች ነገር ብታበድረው ካበደርከው በላይ እንዲመልስልህ አታድርገው”

በወለድ ማበደር

ለአንድ ሰው ማበደርና ያ ሰው ከተበደረው በላይ እንዲመልስ ማስገደድ

የገንዘብ ወለድ -- የትኛውም በወለድ የተሰጠ

“ለአንድ ሰው ገንዘብ፣ ምግብ ወይም የትኛውንም ነገር በምታበድርበት ጊዜ ወለድ አታስከፍለው”

እጅህን በምታሳርፍበት ሁሉ ላይ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በምትሠራሁ ሁሉ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 23:21

ለመፈጸም አትዘግይ

“ስእለትህን ለመፈጸም ረጅም ጊዜ አትውሰድ”

አምላክህ እግዚአብሔር በእርግጥ ከአንተ ይፈልገዋልና

“ምክንያቱም ስእለትህን ካልፈጸምክ አምላክህ እግዚአብሔር ይነቅፍሃል፣ ይቀጣሃልም”

ሳትሳል ብትቀር ግን ኃጢአት አይሆንብህም

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ካልተሳልክ ግን የምትፈጽመው ስእለት የለህምና ኃጢአት አትሠራም” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ከከንፈርህ የወጣውን

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “የተናገርከው ቃል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ለአምላክህ ለእግዚአብሔር እንደተሳልከው

“ታደርገው ዘንድ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር የተሳልከውን ማንኛውንም ነገር”

በአንደበትህ ፈቅደህ ቃል የገባህበትን የትኛውንም ነገር

“ልታደርገው ስለፈለግህ ቃል ስትገባ ሰዎችህ የሰሙህን ነገር ሁሉ”

በአንደበትህ

“ስትናገር ሰዎች የሰሙህን”

Deuteronomy 23:24

የምትፈልገውን ያህል ወይን መብላት ትችላለህ

“ከዚያም እስክትጠግብ ድረስ ወይን በመብላት መደሰት ትችላለህ”

ሆኖም በቅርጫትህ ውስጥ ምንም እንዳትጨምር

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ሆኖም ይዘህ ለመሄድ በከረጢትህ ውስጥ ምንም ወይን አትጨምር” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ወደ ባልንጀራህ የደረሰ ሰብል በምትገባበት ጊዜ

“ሰብሉ ባፈራበት የባልንጀራህ እርሻ መካከል በምታልፍበት ጊዜ”

እሸት መቅጠፍ ትችላለህ

“ከዚያም ከሰብሉ ፍሬ በእጅህ ወስደህ መብላት ትችላለህ”

ነገር ግን በደረሰው የባልንጀራህ ሰብል ላይ ማጭድ አታሳርፍበት

“ነገር ግን የባልንጀራህን የደረሰ ሰብል አጭደህ አትውሰድ”

ማጭድ

ገበሬዎች ስንዴ ለመሰብሰብ የሚጠቀሙበት ስለታም መሣሪያ


Chapter 24

1 አንድ ሰው አንዲት ሴት ካገባ በኋላ አሳፋሪ ነገር አግኝቶባት ባይደሰትባት የፍቺ ወረቀት ጽፎ በመስጠት ከቤቱ አስወጥቶ ይስደዳት። 2 ከቤቱ ከወጣች በኋላ ሌላ ባል ሊታገባ ትችላለች። 3 ሁለተኛ ባሏም እንደዚሁ ጠልቷት የፍቺ ወረቀት በመስጠት ከቤቱ አስወጥቶ ቢሰዳት፥ ወይም ቢሞት፥ 4 ከዚያ በኋላ ፈቶአት የነበረው የመጀመሪያ ባሏ፥ የረከሰች በመሆኗ እንደ ገና መልሶ ሊያገባት አይችልም፤ ይህ በእግዚአብሔር ፊት አስጸያፊ ነው። እግዚአብሔር አምላካችሁ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ ምድር ላይ ኃጢአት አታምጡ። 5 አዲስ ሚስት በቅርብ ጊዜ ያገባ ሰው፥ ለጦርነት አይሂድ ወይም ሌላ ሥራ እንዲሥራ አይገደድ። ለአንድ ዓመት ነጻ ሆኖ እቤቱ ይቆይ፥ ያገባትን ሚስቱን ደስ ያሰኛት። 6 ወፍጮና መጁን ወይም መጁንም እንኳ ቢሆን፥ የብድር መያዣ አድርጋችሁ አትውሰዱ፤ የሰውን ነፍስ መያዣ አድርጎ መውሰድ ይሆናልና። 7 አንድ ሰው ከእስራኤላውያን ወንድሞቹ አንዱን ፈንግሎ በመውሰድ ባሪያ ሲያደርገው ወይም ሲሸጠው ቢገኝ፥ ፈንጋዩ ይሙት። ክፉውን ከመካከላችሁ አስወግድ። 8 የለምጽ ደዌን በተመለከተ ሌዋውያን ካህናት የሚሰጡአችሁን መመሪያ በትክክል ለመፈጸም ጥንቃቄ አድርጉ። እኔ ለእነርሱ የሰጠሁትን ትእዛዝ በጥንቃቄ ተከተሉ። 9 ከግብፅ ከወጣችሁ በኋላ በመንገድ ላይ ሳላችሁ እግዚአብሔር አምላካችሁ በሙሴ እህት በምርያም ላይ ያደረገባትን አስታውሱ። 10 ማናቸውንም ነገር ለባልንጀራችሁ ስታበድሩ መያዣ አድርጎ የሚሰጣችሁን ለመቀበል ወደ ቤቱ አትግቡ። 11 እንንተ ከውጭ ሆናችሁ ጠብቅ፥ ያበደራችሁም ሰው መያዣውን ከቤት ያምጣላችሁ። 12 ሰውየው ድኻ ከሆነ መያዣውን ከእናንተ ዘንድ አታሳድሩበት። 13 መደረቢያውን ለብሶት እንዲያድር ፀሐይ ሳትጠልቅ መልሱለት። ከዚያም ያመሰግናችኋል፤ እግዚአብሔር አምላካችሁ ፊትም የጽድቅ ሥራ ሆኖ ይቆጠርላችኋል። 14 ድኻና ችግረኛ የሆነውን የምንዳ ሠራተኛ እስራኤላዊ ወንድማችሁም ሆነ፥ከከተሞቻችሁ ባንዲቱ የሚኖረውን መጻተኛ አትበዝብዙት፤ 15 የሠራበትን ሒሳብ በዕለቱ ፀሐይ ሳትጠልቅ ክፈሉት፤ ድኻ በመሆኑ በጉጉት ይጠባበቀዋልና። ያለበለዚያ ወደ እግዚአብሔር ይጮኸና ኃጢአት ይሆንባችኋል። 16 አባቶች ስለ ልጆቻቸው፥ ልጆችም ስለ አባቶቻቸው አይገደሉ፤ እያንዳንዱ በራሱ ኃጢአት ይገደል። 17 መጻተኛው ወይም አባት ለሌለው ልጅ ፍትሕ አትንፈጉት፤ ባል የሞትባትንም መደረቢያ መያዣ አታድርጉ። 18 እናንተም በግብፅ ባሪያ እንደ ነበራችሁና እግዚአብሔር አምላካችሁ ከዚያ እንደ ተቤዣችሁ አስታውሱ፤ ይህን እንድታደርጉ ያዘዙአችሁ ለዚህ ነው። 19 የእርሻችሁን ሰብል በምታጭዱበት ጊዜ ተረስቶ የቀረ ነዶ ቢኖር፥ ያን ለመውሰድ ተመልሳችሁ አትሂዱ፤እግዚአብሔር አምላካችሁ በእጃችሁ ሥራ ሁሉ እንዲባርካችሁ ነዶውን ለመጻተኛው፥ አባት ለሌለውና ባል ለሞተባት ተዉ። 20 የወይራ ዛፋችሁን ፍሬ በምታራግፉበት ጊዜ በየቅርንጫፉ ላይ የቀረውን ለመቃረም ተመልሳችሁ አትሂዱ ለመጻተኛ፥ አባት ለሌለውና ባል ለሞተባት ተዉ። 21 የወይን ተክላችሁን ፍሬ ስትሰበስቡ ቃርሚያውን ለመሰብሰብ አትመለሱበት የቀረውን ለመጻተኛው፥ አባት ለሌለውና ባል ለሞተባት ተዉ። 22 በግብፅ ባሮች እንደነበራችሁ አስታውሱ፤ ይህን እንድታደርጉ ያዘዙአሁን ለዚህ ነው።



Deuteronomy 24:1

አንድ ሰው ሚስት ወስዶ በሚያገባበት ጊዜ

“ሚስት ወስዶ” እና “በሚያገባት” የሚሉት ሐረጎች ትርጉማቸው አንድ ነው። አ.ት፡ “አንድ ወንድ አንዲትን ሴት በሚያገባበት ጊዜ” (See: Doublet)

በዐይኖቹ ሞገስን ባታገኝ

እዚህ ጋ “ዐይኖች” የሚወክሉት ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “እንደማይወዳት ከወሰነ” (See: Synecdoche)

አንዳች የሚመቸውን ነገር ስላላገኘባት

“በሆነ ምክንያት ከእርሱ ጋር ሊያቆያት ያለመፈለግ ውሳኔ አድርጓል”

የፍቺ ወረቀት ጽፎ ይስጣት

“ከዚህ በኋላ በጋብቻ ውስጥ እንደሌሉ የሚገልጽ ሕጋዊ ወረቀት ለሚስቱ ይስጣት”

ሄዳ የሌላ ሰው ሚስት እንድትሆን

“ሄዳ ሌላ ሰው እንድታገባ”

Deuteronomy 24:3

ሁለተኛው ባሏ ቢጠላት

“ሁለተኛው ባሏ እንደሚጠላት ቢወስን”

የፍቺ ወረቀት

ይህ ሰውየውና ሴቲቱ ከእንግዲህ በጋብቻ ውስጥ እንዳልሆኑ የሚናገር ሕጋዊ ወረቀት ነው። ይህንን በዘዳግም 24፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

በእጇ ያኑረው

“ለሴቲቱ ይስጣት”

ሚስት አድርጎ የወሰዳት ሰው

“ሴቲቱን ያገባት ሁለተኛው ሰው”

ከረከሰች በኋላ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በፍቺውና እንደገና ሌላ ሰው በማግባቷ ከረከሰች በኋላ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ምድሪቱ በደለኛ እንድትሆን አታድርጋት

ምድር ኃጢአት ልትሠራ እንደምትችል ተደርጋ ተነግሮላታል። አ.ት፡ “በምድሪቱ ዙሪያ በደል እንዳታስፋፋ” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 24:5

አንድ ሰው አዲስ ሚስት በሚወስደበት ጊዜ

“አንድ ሰው በቅርቡ አንዲትን ሴት በሚያገባበት ጊዜ”

የጉልበት ሥራ ለመሥራት እንዲሄድም ቢሆን አይታዘዝ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከቤቱ እንዲርቅና የትኛውንም ዓይነት ሥራ እንዲሠራ ማንም አያስገድደው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በቤቱ ለመሆን ነጻ ይሁን

“በቤቱ ለመኖር ነጻ ይሁን”

Deuteronomy 24:6

ወፍጮ

ክብደት ባላቸው ሁለት ክብ ድንጋዮች እህል በመፍጨት ዱቄት ለመሥራት የሚያስችል መሣሪያ

መጅ

ከወፍጮ ጋር ያለ የላይኛው ክብ ድንጋይ

ያ የሰውን ሕይወት በመያዣነት እንደመውሰድ ይሆናል

“ሕይወት” የሚለው ቃል አንድ ሰው ራሱን በሕይወት ለማቆየት የሚያስፈልገው ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ሰውየው ለቤተሰቡ ምግብ ለማዘጋጀት የሚጠቀምበትን መውሰዱ ነውና” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 24:7

አንድ ሰው ተጠልፎ ቢገን

ይህ የአነጋገር ዘይቤ “አንድ ሰው ቢጠለፍ” እንደማለት ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ሲጠልፍ ብታገኘው” (የአነጋገር ዘይቤ እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

መጥለፍ

አንድን ንጹሕ ሰው ኃይልን በመጠቀም ከቤቱ ወስዶ ማሰር ነው

በእስራኤል ሕዝብ መካከል ከወንድሞቹ አንዱን

“የትኛውንም እስራኤላዊ ወንድሙን”

ያ ሌባ ይሙት

“ከዚያም ሌሎች እስራኤላውያን ያንን ሌባ ስለድርጊቱ በመግደል ይቅጡት”

ክፉን ከመካከልህ ታስወግዳለህ

“ክፉ” የሚለው ቅጽል እንደ ስማዊ ሐረግ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ይህንን ክፉ ነገር ያደረገውን ሰው ከእስራኤላውያን መካከል አስወግደው” ወይም “ይህንን ክፉ ሰው አስወግደው” (ስማዊ ቅጽል የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 24:8

አምላክህ እግዚአብሔር -- ትዝ ይበልህ -- ጥንቃቄ አድርግ -- በጥንቃቄ ጠብቅ

እዚህ ጋ ሙሴ እንደ አንድ ሰው አድርጎ ለእስራኤላውያን ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት ቃላትና “ጥንቃቄ አድርግ” እና “ትዝ ይበልህ” የሚሉት ትዕዛዛት ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

የትኛውንም ለምጽ በሚመለከት ጥንቃቄ አድርግ

“የምትሠቃየው በለምጽ እንደሆነ ልብ በል” ወይም “ለምጽ ይኖርብህ እንደሆነ ልብ በል”

ካህናቱና ሌዋውያኑ የሚያስተምሩህን ለአንተ የተሰጠህን እያንዳንዱን መመሪያ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሰጠሁህን መመሪያዎች በሙሉና ሌዋውያን የሆኑት ካህናቱ እንድታደርገው የሚያስተምሩህን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የሚያስተምሩህን -- እንድታደርገው -- ከግብፅ ከወጣችሁ

እዚህ ጋ ሙሴ ለእስራኤላውያን የሚናገረው እንደ ቡድን ነው፣ ስለዚህ “አንተ” የሚሉት እነዚህ አገባቦች ብዙ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

እኔ እንዳዘዝኳቸው ታደርጋለህ

“እኔ እንዳዘዝኳቸው በትክክል ስለማድረግህ እርግጠኛ ሁን”

እንዳዘዝኳቸው

“እነርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሌዋውያን የሆኑትን ካህናት ነው።

ትዝ ይበልህ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “(የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከግብፅ በመውጣት ላይ እያለህ

“ግብፅን ስትለቅ በነበረበት ጊዜ”

Deuteronomy 24:12

መያዣውን ለራስህ ወስደህ አታሳድርበት

“ኮቱን አታሳድርበት”

መያዣውን

ይህ የሚያመለክተው ብድሩን ባይመልስ በምትኩ ሊሰጥህ ቃል የገባውን ነገር ነው። ይህንን በዘዳግም 24፡10 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

መያዣውን መልስለት

“ብድሩን እንደሚመልስልህ ለማሳየት የሰጠህን መልስለት”

Deuteronomy 24:14

የተቀጠረን አገልጋይ አትጨቁነው

“የተቀጠረን አገልጋይ አትበድለው”

የተቀጠረ አገልጋይ

በየቀኑ ለሥራው የሚከፈለው ሰው

ድኻና ችግረኛ

እነዚህ ሁለት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆኑ ይህ ሰው ራሱን መርዳት የማይችል በመሆኑ ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Doublet)

በከተማህ በሮች ውስጥ

እዚህ ጋ “የከተማ በሮች” ማለት መንደሮች ወይም ከተሞች ማለት ነው። አ.ት፡ “ከከተሞችህ በአንዱ” (See: Synecdoche)

ደሞዙን በየቀኑ ስጠው

“ሰውየው በየቀኑ ማግኘት የሚገባውን ገንዘብ ልትሰጠው ይገባል”

ይህንን ጉዳይ ሳትፈታ ፀሐይ አትጥለቅ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እስራኤላውያኑ ፀሐይ ስትጠልቅ የአዲሱ ቀን ጅማሬ እንደሆነ ያስባሉ። አ.ት፡ “ሥራውን በሠራበት በዚያው ቀን ለሰውየው ልትከፍለው ይገባል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ድኻ በመሆኑ ይጠባበቀዋልና

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ድኻ ስለሆነና ለቀጣይ ቀኑ ምግቡን ለመግዛት በደሞዙ ስለሚተማመን” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

በአንተ ላይ ወደ እግዚአብሕር እንዳይጮህ

“እግዚአብሔርን እንዳይጠራና እንዲቀጣህ እንዳይጠይቀው”

Deuteronomy 24:16

ወላጆች ስለ ልጆቻቸው አይገደሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከልጆቻቸው አንዱ ባደረገው ክፉ ነገር ምክንያት ወላጆችን አትግደል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እንዲሁም ልጆች ስለ ወላጆቻቸው አይገደሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ወላጆቻቸው ባደረጉት ክፉ ነገር ምክንያት ልጆቻቸው አይገደሉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እያንዳንዱ ስለ ገዛ ራሱ ኃጢአት ይገደል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድን ሰው መግደል የሚኖርብህ እርሱ ራሱ ባደረገው ክፉ ነገር ምክንያት ብቻ ነው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 24:17

ከመጻተኛው ወይም አባቱን ካጣው ላይ ኃይልን በመጠቀም ፍትሕን አታስቀርበት

ሙሴ ስለፍትሕ አንድ ጉልበተኛ የሆነ ሰው ከደካማው ላይ በኃይል እንደሚቀማው አካላዊ ቁስ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “የመጻተኛውን ወይም አባቱን ያጣውን ልጅ ፍትሕ አታጓድል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አባቶቻቸውን ያጡ ልጆች

x

Deuteronomy 24:19

ከእርሻህ ላይ የደረሰውን ሰብል በምትሰበስብበት ጊዜ

“በእርሻህ ውስጥ ሰብል በምታጭድበት ጊዜ”

የእህል ነዶ

አንዳንድ ትርጉሞች ይህንን እንደ “እስር” ይተረጉሙታል። ትርጉሞቹ ሁሉ የሚያመለክቱት በቀላሉ ለመሸከም የሚቻል፣ በይበልጥም በአንድ ላይ የታሰሩ የአገዳ እህሎችን ነው።

እርሱ ለመጻተኞች፣ አባቶቻቸውን ላጡ ልጆች ወይም ለመበለቶች ይሁን

የሚታወቀውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “ነዶውን መጻተኛው፣ ወላጆቹን ያጣው ወይም መበለቲቱ እንዲወስዱት ተወው” (See: Ellipsis)

በእጆችህ ሥራ ሁሉ

እዚህ ጋ “እጆች” የሚያመለክቱት ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “በምትሠራው ሥራ ሁሉ” (See: Synecdoche)

የወይራ ዛፍህን በምትነቀንቅበት ጊዜ

የሚታወቀውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “ፍሬው ሲረግፍ ለማንሣት የወይራ ዛፍህን ቅርንጫፎች በምትነቀንቅበት ጊዜ” (See: Ellipsis)

በድጋሚ ወደ ቅርንጫፎቹ አትመለስ

“ከወይራ ዛፉ ላይ እያንዳንዱን ፍሬ አትልቀም”

እርሱ ለመጻተኞች፣ አባቶቻቸውን ላጡ ልጆች ወይም ለመበለቶች ይሆናል

የሚታወቀውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “በቅርንጫፎቹ ላይ የሚቀሩት የወይራ ፍሬዎች መጻተኞች፣ ወላጆቻቸውን ያጡና መበለቶች ለቅመው የሚወስዷቸው ናቸው” (See: Ellipsis)

Deuteronomy 24:21

የቀረው ለመጻተኞች፣ አባቶቻቸውን ላጡ ልጆች እና ለመበለቶች ይሆናል

“የማትለቅመው የወይን ፍሬ ለመጻተኛው፣ አባቱን ላጣውና ለመበለቲቱ ይሆናል”

ለመጻተኞች፣ አባቶቻቸውን ላጡ ልጆች እና ለመበለቶች ይሆናል

እነዚህ የሚያመለክቱት የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ነው። አ.ት፡ “ለመጻተኞች፣ ወላጆቻቸውን ላጡና ለመበለቶች” (See: Generic Noun Phrases)

ትዝ ይበልህ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አስታውስ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 25

1 በሰዎች መካከል ጠብ ቢነሣ ወደ ፍርድ አደባባይ ቢሄዱ፥ ዳኞች ተበዳይን ነጻ፥ በዳይን ግን ጥፋተኛ፥ በማድረግ የፍርድ ውሳኔ ይስጡ። 2 በደለኛው ሰው መገረፍ የሚገባው ሆኖ ከተገኘ፥ ዳኛው መሬት ላይ ያጋድመው፥ ለጥፋቱ ተመጣጣኝ የሆነ ግርፋት እርሱ ባለበት ይገረፍ። 3 ሆኖም ግርፋቱ ከአርባ የሚበልጥ አይሁን፥ ከዚህ ካለፈ ግን እስራኤላዊ ወንድማችሁ በፊታችሁ የተዋረደ ይሆናል። 4 እህል እያበራየ ያለውን በሬ አፉን አትሰሩ። 5 ወንድማማቾች በአንድነት ቢኖሩና፥ ከእነርሱ አንዱ ወንድ ልጅ ሳይወልድ ቢሞት፥የሟቹ ሚስት ከቤተ ሰቡ ውጭ ባል ማግባት የለባትም። የባሏ ወንድም ይውሰዳትና ያግባት፤ የዋርሳነት ግዴታውንም ይፈጽምላት። 6 በመጀመሪያ የምትወልደውም ልጅ ስሙ ከእስራኤል ፈጽሞ እንዳይጠፋ በሟች ወንድሙ ስም ይጠራ። 7 ሆኖም ግን አንድ ሰው የወንድሙን ሚስት ለማግባት ባይፈልግ ሴትዮዋ በከተማዋ በር ወዳሉት ሽማግሌዎች ሄዳ የባለቤቴ ወንድም የወንድሙን ስም በእስራኤል ለማስጠራት አልፈለገም፥ የዋርሳነት ግዴታውንም አልፈጸመልኝም ትበላቸው። 8 ከዚያም የከተማው ሽማግሌዎች ያን ሰው ጠርተው ያነጋግሩት እርሱም እርሷን ላገባት አልፈልግም ብሎ በሐሳቡ ቢጸና፥ 9 የወንድሙንም ሚስት በሽማግሌዎች ፊት ወደ እርሱ ቀርባ፥ የአንድ እግሩን ጫማ በማውለቅ በፊቱ ላይ ትትፋበትና የወንድሙን ቤት ማይሠራ ሰው ላይ እንዲህ ያለው ድርጊት ይፈጸምበታል ትበል። 10 የዚያም ሰው የዘር ሐረግ በእስራኤል ዘንድ ጫማው የወለቀበት ቤት ተብሎ ይታወቃል። 11 ሁለት ሰዎች ቢደባደቡ፥ የአንደኛው ሚስት ባሏን ከደብዳቢው እጅ ለማስጣል መጥታ እጇን ዘርግታ ብልቱን ብትይዘው 12 ፥እጇን ቁረጡ አትራሩላት። 13 በከረጢታችሁ ውስጥ ከባድና ቀላል የሆኑ ሁለት የተለያዩ ሚዛኖች አይኑሩአችሁ። 14 በቤታችሁም ውስጥ ትልቅና ትንሽ የሆኑ ሁለት የተለያዩ መስፈሪያዎች አይኑሩአችሁ። 15 እግዚአብሔር አምላካችሁ በሚሰጣችሁ ምድር ዕድሜአችሁ እንዲረዝም ትክክለኛና የታመነ ሚዛንና መስፈሪያ ይኑራችሁ። 16 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንዲህ ያሉትን ጽድቅ ያልሆን ነገሮች የሚፈጽመውንና የሚያምታታውን ሁሉ ይጸየፈዋልና። 17 ከግብፅ በወጣችሁ ጊዜ አማሌቅ በመንገድ በእናንተ ላይ ያደረጉባችሁን አስታውሱ፤ 18 ደክማችሁና ዝላችሁ በነበራችሁበት ጊዜ በጉዞ ላይ አግኝቶአሁ ከኋላ ያዘግሙ የነበሩትን ሁሉ ገደሉ፤ እግዚአቤርንም አልፈሩም። 19 እግዚአብሔር አምላካችሁ ርስት አድርጎ በሚሰጣችሁ ምድር ዙሪያ ካሉት ጠላቶቻችሁ ሁሉ ባሳረፋችሁ ጊዜ ከሰማይ በታች ያለውን የአማሌቅን መታሰቢያ ደምስሱ፤ ከቶ እንዳትረሱ!



Deuteronomy 25:1

በደለኛው ሰው መገረፍ የሚገባው ከሆነ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ዳኛው በደለኛውን ሰው እንዲገርፉት ካዘዛቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በፊቱ ይገረፍ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሲገርፉት ያያቸዋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ስለ ወንጀሉ የታዘዘውን የግርፋት ቁጥር

“ስላደረገው ክፉ ሥራ ባዘዘው ቁጥር ልክ”

Deuteronomy 25:3

ዳኛው አርባ ግርፋት ሊሰጠው ይችላል

“ዳኛው በደለኛውን ሰው 40 ጊዜ እንዲገርፉት ሊነግራቸው ይችላል” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሆኖም ከዚያ ቁጥር መብለጥ አይኖርበትም

“ሆኖም ዳኛው ከ40 ጊዜ በላይ እንዲገረፍ ማዘዝ አይኖርበትም”

ከዚያ ቁጥር ካለፈና ተጨማሪ ግርፋት የሚገርፈው ከሆነ

“ዳኛው ከ40 ጊዜ በላይ እንዲገርፉት የሚያዛቸው ከሆነ”

ያን ጊዜ እስራኤላዊው ወንድምህ በዐይኖችህ ፊት የተዋረደ ይሆናል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ያን ጊዜ በእስራኤል ሕዝብ ሁሉ ፊት እስራኤላዊውን ወንድምህን ያዋርደዋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በዐይኖችህ ፊት የተዋረደ ይሆናል

እዚህ ጋ ስለሚያዩት ነገር አጽንዖት ለመስጠት ሕዝቡ በ “ዐይኖቻቸው” ተወክለዋል። አ.ት፡ “ተዋርዷል፣ እናንተ ሁላችሁም አይታችሁታል” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 25:5

ወንድማማቾች በአንድነት የሚኖሩ ከሆነ

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች፣ 1) “ወንድማማቾች በአንድ ንብረት ላይ የሚኖሩ ከሆነ” ወይም 2) “ወንድማማቾች ተቀራርበው የሚኖሩ ከሆነ”

ያን ጊዜ የሟቹ ሰው ሚስት ሌላ ሰው ማግባት አይኖርባትም

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ያን ጊዜ የሟች ቤተሰቦች መበለቲቱ ሌላ ሰው እንድታገባ መፍቀድ የለባቸውም” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የዋርሳነቱን ተግባር ይፈጽምላት

“የሟች ወንድም እንዲያደርግ የሚጠበቅበትን ያድርግ”

በሟች ወንድሙ ስም ይጠራል

“ስም” የሚለው ቃል የሰውየውን የቤተሰብ ሐረግ የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የሟች ወንድሙ የቤተሰብ ሐረግ ይቀጥላል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስሙ ከእስራኤል እንዳይጠፋ

“ስም” የሚለው ቃል የሰውየውን የቤተሰብ ሐረግ የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የቤተሰቡ ሐረግ ከእስራኤል እንዳይጠፋ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 25:7

ወደ በሩ ወደ ሽማግሌዎች ትሂድ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ሽማግሌዎች በጉዳዮች ላይ ወደሚዳኙበት ወደ ከተማው በር ትሂድ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ለወንድሙ ስም ለማቆም እምቢ ቢል

እዚህ ጋ “ስም” የሚያመለክተው በተወላጆቹ አማካይነት የአንድን ሰው መታሰቢያ ነው። አ.ት፡ “ለወንድሙ ወንድ ልጅ ለመስጠት እምቢ ቢል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የዋርሳነቱን ተግባር አልፈጸመልኝም

“እኔን በማግባት ከዋርሳ የሚጠበቅበትን ተግባር አልፈጸመም”

ልወስዳት አልፈልግም

“ላገባት አልፈልግም”

Deuteronomy 25:9

በሽማግሌዎቹ ፊት ወደ እርሱ ትቅረብ

“በዚያ ያሉ ሽማግሌዎች እያዩአት ተራምዳ ትቅረበው”

የወንድሙን ቤት በማይሠራ

እዚህ ጋ “ቤት” የቤተሰብ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ለወንድሙ ወንድ ልጅ የማይሰጥና የወንድሙን የቤተሰብ ሐረግ የማያስቀጥል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስሙ በእስራኤል ይጠራል

“በእስራኤል ያሉ ሰዎች ቤተሰቡን እንደ -- ያውቃሉ”

ጫማው እንዲወልቅ የተደረገበት ሰው ቤት

እዚህ ጋ ጫማ የማውለቁ ምሳሌ ወንድምየው ከሟች ወንድሙ ሀብት ምንም እንደማይወስድ ማሳያ ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። ደግሞም ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል. አ.ት፡ “የወንድሙ ሚስት ጫማውን ከእግሩ ያወለቀችበት ሰው ቤት” ወይም “የወንድሙን ሚስት ያላገባው ሰው ቤተሰብ” ወይም “ሁሉም ሰው የሚንቀው ቤተሰብ” ወይም “አሳፋሪው ቤተሰብ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 25:11

ከደብዳቢው እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” ኃይልን ወይም ቁጥጥርን ያመለክታል። አ.ት፡ “ደብዳቢው እንደ ገና እንዳይደበድበው” ወይም “እርሱን ከሚመታው ሰው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዐይንህ አይራራ

እዚህ ጋ “ዐይን” ማለት ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “አትዘንላት” ወይም “ምሕረት አታድርግላት” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 25:13

በቦርሳህ ውስጥ ትልቅና ትንሽ የሆኑ የተለያዩ ሚዛኖች አይኑሩህ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። በተጨማሪም የሚታወቀውን መረጃ ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “ነገሮችን በምትገዛበት ጊዜ ከምትናገረው የሚበልጥን ሚዛን በመጠቀም፣ በምትሸጥበት ጊዜ ደግሞ ከምትናገረው ያነሰ ሚዛን በመጠቀም ሰዎችን አታጭበርብር” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information and Ellipsis)

ሚዛኖች

ሚዛኖች አንድ ነገር ምን ያህል እንደሚከብድ ለማወቅ መለኪያው ላይ የሚቀመጡ ድንጋዮች ነበሩ

በቤትህ ውስጥ ትልቅና ትንሽ የሆኑ የተለያዩ ሚዛኖች አይኑሩህ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ በተጨማሪም፣ የሚታወቀውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “ነገሮችን በምትገዛበት ጊዜ ከምትናገረው የሚበልጥ መለኪያ በመጠቀም፣ እንዲሁም በምትሸጥበት ጊዜ ከምትናገረው የሚያንስ መለኪያ በመጠቀም ሰዎችን ማጭበርበር የለብህም። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information and Ellipsis)

መለኪያዎች

መለኪያ አንድ ነገር ምን ያህል እንደሆነ የሚለካበት ቅርጫት ወይም ሌላ መያዣ ነበር።

Deuteronomy 25:15

ልክና ተገቢ

“ትክክል እና አግባብነት ያለው”

ሚዛን -- መለኪያ

እነዚህን ቃላት በዘዳግም 25፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ቀኖችህ እንዲረዝሙ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ረጅም ዘመን እንድትኖር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እንደዚህ ያሉትን ነገሮች ለሚያደርጉ፣ በእምነት አጉዳይነት ለሚያደርጉ ሁሉ

“የተለያየ መጠን ያላቸውን ሚዛኖችና መለኪያዎችን በመጠቀም ሰዎችን የሚያጭበረብሩ ሁሉ”

Deuteronomy 25:17

አማሌቅ ያደረገብህ ትዝ ይበልህ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን “አማሌቅ” አማሌቃውያን ሰዎችን የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “አማሌቃውያን ያደረጉብህን አስታውስ” (የአነጋገር ዘይቤ፣ ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ እና ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በወጣህ ጊዜ

እዚህ ጋ “አንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

በመንገድ ላይ እንዴት እንደተገናኘህ

“በጉዞ ላይ እያለህ እንዴት እንደተገናኙህ”

ከኋላ የነበራችሁትን አጠቋችሁ

“የኋላ መስመር ላይ የነበሩትን ሰዎችህን አጠቃ”

ከበስተኋላህ የደከሙትን ሁሉ

“በኋለኛው መስመር ላይ ደካሞች የነበሩትን ሰዎች በሙሉ”

ዝለትና ድካም

እነዚህ ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆኑ ሕዝቡ ምን ያህል ደክመው እንደነበሩ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “ደክመውና ዝለው” (See: Doublet)

ለእግዚአብሔር ክብርን አልሰጠም

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔርን ቅጣት አልፈራም” ወይም “እግዚአብሔርን አላከበረም” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

የአማሌቅን መታሰቢያ ከሰማይ በታች ደምስስ

“ከእንግዲህ ማንም እንዳያስታውሳቸው አማሌቃውያንን በሙሉ ግደላቸው”


Chapter 26

1 እግዚአብሔር አምላካችሁ ርስት አድርጎ ወደ ሚሰጣችሁ ምድር ስትገቡ፥ ስትወርሱአትና ስትኖሩባት፤ 2 እግዚአብሔር አምላካችሁ ከሚሰጣችሁ ምድር ከሁሉም የመጀመሪያ ፍሬ ውሰዱት። ከዚያም በቅርጫት ውስጥ አድርጉትና እግዚአብሔር አምላካችሁ ለስሙ ማደሪያ እንዲሆን ወደሚመርጠው ስፍራ ሂዱ። 3 በዚያን ወቅት ወደ ሚያገለግለው ካህን ሄዳችሁ ፦ እግዚአብሔር ለእኛ ሊሰጠን ለአባቶቻችን ወደ ማለላቸው ምድር እንደ ገባሁ ዛሬ እግዚአብሔር አምላካችሁን ለማምስገን እቀባለለሁ በለው። 4 ካህኑም ቅርጫቱን ከእጃችሁ ተቀብሎ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ መሠዊያ ፊት ለፊት ያኖረዋል። 5 እናንተም በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት እንዲህ ብላችሁ ትናገራላችሁ፦ አባቴ ዘላን ሶርያዊ ነበር፤ ከጥቂት ሰዎችም ጋር ወደ ግብፅ ወረደ፤ በዚያም ተቀመጠ፤ ታላቅ፥ ኃያልና ቁጥሩ የበዛ ሕዝብ ሆነ። 6 ግብፃውያንም በመጥፎ ሁኔታ እንገላቱን፥ አሠቃዩንም። እንደ ባሪያ ከባድ ሥራ እንድንሠራ አደረጉን። 7 ከዚያ በኋላ ወደ አባቶቻችን አምላክ ወደ እግዚአብሔር ጮኸን፥ እርሱም ጩኸታችንን ሰማ፤ መከራችንን፣ ድካማችንንና የተፈጸመብንን ግፍ ተመለከተ። 8 ከዚህ የተነሣ እግዚአብሔር በብርቱ እጅና በተዘረጋው ክንዱ፥ በታላቅ ድንጋጤና ታምራት በምልክትና በድንቅ ከግብፅ አወጣን፤ 9 ወደዚህም ስፍራ አመጣን፥ ማርና ወተት የምታፈሰውን ይህችን ምድር ሰጠን። 10 እግዚአብሔር ሆይ እነሆ፥ አንተ ከሰጠኸኝ ከምድሪቱ የመጀመሪያ ፍሬ አምጥቻለሁ፤ ቅርጫቱንም በአምላክህ በእግዚአብሔር ፊት አኑራሃው አምልከው፤ 11 ለአንተና ለቤትህ ባደረገው መልካም ነገር አንተ፥ ሌዋውያንና መጻተኞች በእግአብሔር በአምላክህ ፊት ደስ ይበላችሁ። 12 የአሥራት ዓመት የሆነውን የሦስተኛውን ዓመት ፍሬ አንድ አሥረኛ ለይታችሁ ካወጣችሁ በኃላ በየከተሞቻችሁ ውስጥ በልተው እንዲጠግቡ፥ ለሌዋዊው፥ ለመጻተኛው፥አባት ለሌለውና ባል ለሞተባቸው ስጡአቸው። 13 ከዚያ በኋላ ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር እንዲህ በል፦ በሰጠኸኝ ትእዛዝ መሠረት ለእግዚአብሔር የተቀደሰውን ከቤቴ አምጥቼ ለሌዋዊው፥ ለመጻተኛው፥ አባት ለሌለውና ባል ለሞተባት ሰጥቻለሁ። ከትእዛዝህ አልወጣሁም፤ አንዱንም አልረሳሁም። 14 በሐዘን ላይ ሳለሁ፥ ከተቀደሰው ክፍል ላይ ምንም አልበላሁም ባልነጻሁበትም ጊዜ ከዚህ ላይ ያነሣሁትምና ለሙታን ያቀረብሁት ምንም ነገር የለም። አምላኬን እግዚአብሔርን ታዝዣለሁ፥ ያዘዝኸኝንም ሁሉ ፈጽሜአለሁ። 15 ከቅዱስ ማደሪያ ሆነህ ከሰማይ ተመልከት፥ ሕዝብህን እስራኤልንና ለአባቶቻችን በማለህላቸው መሠረት፥ ለእኛ የሰጠኸንን ይህችን ማርና ወተት የምታፈሰውን ምድር ባርክ። 16 እግዚአብሔር አምላካችሁ ይህን ሥርዓትንና ሕግን ትጠብቁ ዘንድ ዛሬ ያዝዛችኋል፤ እናንተም በፍጹም ልባችሁ በፍጹምም ነፍሳችሁ ትፈጽሙት ዘንድ ተጠንቀቁ። 17 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደሆነ በመንገዱም እንደምትሄዱ፥ ሥርዓቱን፥ ትእዛዙንና ሕጉን እንደምትጠብቁ እንደምትታዘዙለት በዛሬው ዕለት ተናግራችኋል። 18 እግዚአብሔር በሰጣችሁ ተስፋ መሠረት እንንተ ሕዝቡና ርስቱ መሆናችሁን ትእዛዙንም ሁሉ እንደምትጠብቁ በዛሬው ዕለት ተናግሮአል፤ 19 ከፈጠራቸው ሕዝቦች ሁሉ በላይ ለማመስገን፥ ለማክበረና ከፍ ለማድረግና በሰጠውም ተስፋ መሠረት ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ ቅዱስ ሕዝብ እንደምትሆኑ ማረጋገጫ ሰጥቶአል።



Deuteronomy 26:1

ከመጀመሪያው ምርትህ ሁሉ ጥቂቱን

“ከምርትህ በኩራት ጥቂቱን” ወይም “ከመጀመሪያው የሰብል ምርትህ ጥቂቱን”። ይህ “መጀመሪያ” የአንድ ደረጃን ማሳያ ቁጥር ነው። (ደረጃን ማሳያ ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 26:5

ቅድመ ቅድም አያቴ ተቅበዝባዥ አራማዊ ነበር

ይህ እስራኤላዊ ወንድ ቅርጫቱን በሚያቀርብበት ጊዜ መናገር የሚኖርበት የዐረፍተ ነገሩ መጀመሪያ ነው።

ተቅበዝባዥ አራማዊ

ይህ የእስራኤላውያኑ ሁሉ ቅድመ ቅድም አያት የነበረውን ያዕቆብን ያመለክታል። እርሱ ለብዙ ዓመታት በሶሪያ በሚገኝ በአራም ናሃሪም ይኖር ነበር።

በዚያ ቆየ

“ቀሪ ሕይወቱን በዚያ ኖሯል”

በዚያ እርሱ -- ሆነ

“እርሱ” የሚለው ቃል “የያዕቆብን ተወላጆች” የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ታላቅ፣ ኃያል

በመሠረቱ እነዚህ ቃላት የሚሉት አንድ ነገር ነው። እስራኤል ብዙና ኃይለኛ ሕዝብ መሆኑ ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “በጣም ታላቅ” (See: Doublet)

Deuteronomy 26:6

ከፉብን፣ አሰቃዩንም

በመሠረቱ እነዚህ ሁለት ሐረጎች የሚሉት አንድ ነገር ነው። ግብፃውያን የጭካኔ ተግባር እንደ ፈጸሙባቸው አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Doublet)

አደረገብን

እዚህ ጋ “እኛ” የሚያመለክተው በግብፅ ይኖሩ የነበሩትን የእስራኤል ሕዝብ ነው። ተናጋሪው በግብፅ ቢኖርም ባይኖርም ራሱን ከሕዝቡ አንዱ አድርጎ ይጨምራል። (See: Inclusive “We”)

ድምፃችንን ሰማ

እዚህ ጋ “ድምፅ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው እና ጩኸቱን ወይም ጸሎቱን ነው። አ.ት፡ “ጩኸታችንን ሰማ” ወይም “ጸሎታችንን ሰማ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስቃያችንን፣ ልፋታችንን እና መጨቆናችንን

“ግብፃውያን ያሰቃዩን የነበረውን፣ ስንሠራው የነበረውን በጣም ከባድ የሆነውን ሥራ እና ግብፃውያኑ ይጨቁኑን የነበረውን”

Deuteronomy 26:8

እግዚአብሔር አመጣን

እዚህ ጋ “እኛ” የሚያመለክተው በግብፅ ይኖሩ የነበሩትን የእስራኤል ሕዝብ ነው። ተናጋሪው በግብፅ ቢኖርም ባይኖርም ራሱን ከሕዝቡ አንዱ አድርጎ ይጨምራል። (See: Inclusive “We”)

በብርቱ እጅ፣ በተዘረጋች ክንድ

እዚህ ጋ “ብርቱ እጅ” እና “የተዘረጋች ክንድ” የእግዚአብሔርን ኃይል የሚያመለክቱ ዘይቤአዊ አነጋገሮች ናቸው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡34 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ብርቱ ኃይሉን በማሳየት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በታላቅ ማስደንገጥ

“ያዩአቸውን ሰዎች በሚያስፈሩ ድርጊቶች”

ወተትና ማር የምታፈስ ምድር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ይህንን በዘዳግም 6፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት፡ አ.ት፡ “ብዙ ወተትና ማር የሚፈስባት ምድር” ወይም “ከብት ለማርባትና ለእርሻ ምርጥ የሆነች ምድር”

Deuteronomy 26:10

ከአዝመራው የመጀመሪያውን

“ከአዝመራው የመጀመሪያውን ፍሬ” ወይም “ከአዝመራው የመጀመሪያውን ሰብል”

አስቀምጠው

“ቅርጫቱን አስቀምጠው”

አምላክህ እግዚአብሔር ባደረገልህ መልካም ነገር ሁሉ ደስ ይበልህ

“አምላክህ እግዚአብሔር ስላደረገልህ መልካም ነገሮች ሁሉ ደስ ይበልህ፣ አመስግንም”

Deuteronomy 26:12

በሦስተኛው ዓመት

ይህ “ሦስተኛ” የሦስት ደረጃን አመልካች ቁጥር ነው። የእስራኤል ሕዝብ በየሦስት ዓመቱ ከአዝመራው አንድ አሥረኛውን ለድኾች ይሰጡ ነበር። (ደረጃን አመልካች ቁጥር የሚለውን ተመልከት)

አባቶቻቸውን ያጡ

እነዚህ ሁለቱም ወላጆቻቸው የሞቱባቸውና የሚንከባከባቸው ዘመድ የሌላቸው ልጆች ናቸው።

መበለት

ይህ ማለት ባል የሞተባትና በእርጅናዋ ጊዜ የሚንከባከብ ልጅ የሌላት ሴት ማለት ነው።

በከተማህ በሮች ውስጥ ብላ፣ ጥገብም

እዚህ ጋ “በሮች” ማለት መንደሮች ወይም ከተሞች ማለት ነው። አ.ት፡ “እነዚያ በመንደርህ ውስጥ የሚኖሩት የሚበሉት በቂ ምግብ እንዲኖራችው” (See: Synecdoche)

ከ -- አውጥቻችኋለሁ

እነዚህ እስራኤላዊው እንዲለው የሚጠበቅበት የሌላው አነጋገር የመጀመሪያ ቃላት ናቸው።

አልረሳኋቸውም

ይህ ማለት የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት በሙሉ ታዟል።

Deuteronomy 26:14

በለቅሶዬ ጊዜ ከእርሱ ምንም አልበላሁም

“ባለቀስኩበት ወቅት የትኛውንም አስራት አልበላሁም”

ባልነጻሁበት ጊዜ

እዚህ ጋ “ያልነጻ” ማለት በሕጉ መሠረት ንጹሕ ያልሆነ ሰው ማለት ነው። ንጹሕ ያልሆነ ሰው ለእግዚአብሔር የሚሰጠውን አስራት እንዲነካ እግዚአብሔር አይፈቅድለትም”። የዚህ አነጋገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በሕጉ መሠረት ንጹሕ ባልነበርኩበት ጊዜ” ወይም “ልነካው እንደማልችል ሕጉ በሚናገርበት ጊዜ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

የአምላኬን የእግዚአብሔርን ድምፅ ሰምቻለሁ፤ እንዳደርገው ያዘዝከኝን ሁሉንም ነገር ታዝዣለሁ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” እግዚአብሔር ለተናገረው የዋለ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። ሁለቱም አነጋገሮች ተመሳሳይ ትርጉም ይጋራሉ። ሰውየው የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት በሙሉ ስለመታዘዙ አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Parallelism የሚለውን ተመልከት))

ከምትኖርበት ከቅዱሱ ስፍራ፣ ከሰማይ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች የሚሉት ተመሳሳይ ነገር ነው። አ.ት፡ “ከቅዱስ ማደሪያህ፣ ከሰማይ” (See: Dou- blet)

ወተትና ማር የምታፈስ ምድር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ይህንን በዘዳግም 6፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ብዙ ወተትና ማር የሚፈስባት ምድር” ወይም “ከብት ለማርባትና ለእርሻ ምርጥ የሆነች ምድር”

Deuteronomy 26:16

በሙሉ ልብህና በሙሉ ነፍስህ

እዚህ ጋ “ልብ” እና “ነፍስ” የአንድን ሰው ውስጣዊ ማንነት የሚመለከቱ ፈሊጣዊ አነጋገሮች ናቸው። እነዚህ ሁለት ሐረጎች በአንድ ላይ “ሙሉ በሙሉ” ወይም “በቅንነት” ለማለት ጥቅም ላይ ውለዋል። ይህንን በዘዳግም 4፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

በመንገዶቹ ትሄድና ሥርዓቱን፣ ትዕዛዛቱን እና ሕጉን ትጠብቅ ዘንድ፣ ድምፁንም ትሰማ ዘንድ

እዚህ ጋ “መሄድ”፣ “መጠበቅ” እና “መስማት” የሚሉት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው። እዚህ ጋ “ድምፅ” የሚያመለክተው እግዚአብሔር የተናገረውን ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ያዘዘው ሁሉ ሙሉ በሙሉ እንድትጠብቅ” (See: Parallelism and Metonymy)

Deuteronomy 26:18

የራሱ ርስት የሆነን ሕዝብ

“የእርሱ የሚሆንን ሕዝብ”


Chapter 27

1 ሙሴና የእስራኤል አለቆች ሕዝቡን እንዲህ ብለው አዘዙ፦ ዛሬ የማዛችሁን እነዚህን ትእዛዞች ሁሉ ጠብቁ። 2 አምላካችሁ እግዚአብሔር ወደሚሰጣችሁ ምድር ለመግባት ዮርዳኖስን በተሻገራችሁ ጊዜ ጥቂት ትልልቅ ድንጋዮችን አቁሙና በኖራ ለስኑአቸው። 3 የአባቶቻችሁ አምላክ እግዚአብሔር በሰጣችሁ ተስፋ መሠረት ማርና ወተት ወደምታፈሰው፥ አምላካችሁ እግዚአብሔር ወደሚሰጣችሁ ምድር ለመግባት ዮርዳኖስን ስትሻገሩ የዚህን ሕግ ቃላት ሁሉ ጻፉባቸው። 4 ዮርዳኖስን እንደ ተሻገራችሁም ዛሬ ባዘዙአችሁ መሠረት እነዚህን ድንጋዮች በጌባል ተራራ ላይ ትከሉአቸው በኖራም ለስኑአቸው። 5 እዚያም ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ የድንጋይ መሠዊያ ሥራ፥ በድንጋዮቹም ላይ ማናቸውንም የብረት መሣሪያ አታሳርፉባቸው። 6 የእግዚአብሔር የአምላካችሁን መሠዊያ ካልተጠረበ ድንጋይ ሥሩ፥ በላዩም ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ የሚቃጠል መሥዋዕት አቅርቡበት። 7 በላዩም የኅብረት መሥዋዕት ሠዉ፤ ብሉም፤ በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ፊት ደስ ይበላችሁ። 8 በድንጋዮቹም ላይ የዚህ ሕግ ቃላት ሁሉ ግልጽ አድርጋችሁ ጻፉባቸው። 9 ሙሴና ሌዋውያን ካህናትም፥ ለእስራኤል ሁሉ እንዲህ ብላችሁ ተናገሩ፦ እስራኤል ሆይ፥ ጸጥ ብላችሁ አድምጡ! እናንተ ዛሬ የእግዚአብሔር የአላካችሁ ሕዝብ ሆናችኋል። 10 ስለዚይም እግዚአብሔር አምላካችሁን ታዘዙ፥ ዛሬ የሚሰጣችሁን ትእዛዙንና ሥርዓቱን ጠብቁ። 11 ሙሴ በዚያኑ ዕለት ሕዝቡን እንዲህ ብሎ አዘዘ፦ 12 ዮርዳኖስን በተሻገራችሁ ጊዜ ስምዖን ፥ ሌዊ፥ ይሁዳ፥ ይሳኮር፥ ዮሴፍና ብንያም ወገኖች ሕዝቡን ለመባረክ በገሪዛን ተራራ ላይ ይቁሙ። 13 ሮቤል፥ ጋድ፥ አሴር፥ ዛብሎን፥ ዳንና ንፍታሌምወገኖች በጌባል ተራራ ላይ ለመርገም ይቁሙ። 14 ሌዋውያን ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ለእስራኤል ሕዝብ ሁሉ እንዲህ ብለው ይናገሩ፦ 15 ጥበበኛ የሠራውን በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ የሆነውን ምስል የሚቀርጽ ወይም ጣዖትን የሚያበጅ በስውርም የሚያቆም ሰው የተረገመ ይሁን። ሕዝብም ሁሉ፥ አሜን ይበል። 16 አባቱን ወይም እናቱን የሚያቃልል የተረገም ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ፤ አሜን ይበል። 17 የባልንጀራውን የድንበር ድንጋይ ከቦታው የሚያንቀሳቅስ የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ፤ አሜን ይበል። 18 ዐይነ ስዉርን በተሳሳተ መንገድ የሚመራ የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ፤ አሜን ይበል። 19 በመጻተኛው፥ አባት በሌለውና ባል በሞተባት ላይ ፍትሕ የሚያዛባ የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ፤ አሜን ይበል። 20 ከአባቱ ሚስት ጋር የሚተኛ የተረገመ ይሁን፤ የአባቱን መኝታ ያረክሳልና። ሕዝቡም ሁሉ፤ አሜን ይበል። 21 ከማናቸውም እንስሳ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚያደርግ የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ፤ አሜን ይበል። 22 የአባቱ ወይም የእናቱ ልጅ ከሆነችው ከእኅቱ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚፈጽም የተረገመ ይሁን። 23 ሕዝቡም ሁሉ አሜን ይበል። ከሚስቱ እናት ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት የሚፈጽም የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ አሜን ይበል። 24 በድብቅ ባልንጀራውን የሚገድል የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ አሜን ይበል። 25 ንጹሕውን ሰው ለመግደል ጉቦ የሚቀበል የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ አሜን ይበል። 26 የዚህን ሕግ ቃሎች በመፈጸም የማይጸና የተረገመ ይሁን። ሕዝቡም ሁሉ አሜን ይበል።



Deuteronomy 27:1

ዛሬ የማዛችሁን -- ትሻገራላችሁ

ሙሴ እንደ አንድ ቡድን አድርጎ የሚናገረው ለእስራኤላውያን ነው፣ ስለዚህ በሁለቱም አገባብ “አንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

የማዛችሁን

እዚህ ጋ “እኔ” የሚያመለክተው ሙሴን ነው። ሽማግሌዎቹ ከሙሴ ጋር ተስማምተው በዚያ አሉ፣ ሆኖም ብቸኛው ተናጋሪ እርሱ ነው።

በኖራ ቅባው

ይህ ዓይነቱ በአብዛኛው የኖራ፣ አሸዋና ውሃ ድብልቅ ሲሆን በአንድ ነገር ላይ የሚቀባ ነው። ሲደርቅ አንድ ሰው በላዩ ላይ መጻፍ እንዲችል ጠንካራና ለስላሳ ገጽታ ይኖረዋል። አ.ት፡ “ቅባቸው” ወይም “ልትጽፍባቸው እንዲያስችሉህ አድርግ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ወተትና ማር የምታፈስ ምድር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ይህንን በዘዳግም 6፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ብዙ ወተትና ማር የሚፈስባት ምድር” ወይም “ለከብት እርባታና ለእርሻ ምርጥ የሆነች ምድር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 27:4

እኔ የማዝህን -- ስትሻገር -- አስቀምጥ

ሙሴ ለእስራኤላውያን የሚናገረው እንደ ቡድን አድርጎ ነው፣ ስለዚህ “አንተ” የሚልበት አገባብና “አስቀምጥ” የሚለው ትዕዛዝ ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

በኖራ ቅባው

“ቅባቸው” ወይም “ልትጽፍባቸው እንዲያስችሉህ አድርግ”። ይህንን በዘዳግም 27፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የጌባል ተራራ

ይህ በሴኬም አቅራቢያ የሚገኝ ተራራ ነው። እርሱን በዘዳግም 11፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ድንጋዮቹን ለመጥረብ ምንም ዓይነት የብረት መሣሪያ አትጠቀም

ይህ ድንጋዮቹን በማለስለስ በተሻለ ሁኔታ በአንድ ላይ እንዲገጣጠሙ ለማድረግ የሚያገለግሉ መሮዎችን ያመለክታል። የዚህ አነጋገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የመሠዊያውን ድንጋዮች በብረት መሣሪያ አትጥረባቸው” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 27:6

ባልተጠረቡ ድንጋዮች

ማንም በብረት መሣሪያ ያልጠረባቸው በተፈጥሮ ቅርጻቸው ያሉ ድንጋዮች

በድንጋዮቹ ላይ ጻፍባቸው

ይህ በኖራ ተቀብተው በጌባል ተራራ ላይ የሚቆሙትን ድንጋዮች ያመለክታል። ይህንን በዘዳግም 27፡12 እና 27፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 27:9

የአምላክህን የእግዚአብሔርን ድምፅ ታዘዝ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር እርሱ የሚናገረውን ያመለክታል። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር የሚናገረውን ታዘዝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እኔ የማዝህን

ሙሴ እያዘዘ ነው። ሌዋውያኑ ከሙሴ ጋር በመስማማት በዚያ ይገኛሉ፣ ሆኖም የሚናገረው እርሱ ብቻ ነው።

Deuteronomy 27:11

እነዚህ ነገዶች

እዚህ ጋ “ነገዶች” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው የስምዖን፣ ሌዊ፣ ይሁዳ፣ ይሳኮር፣ ዮሴፍ፣ እና ብንያም ነገድ ሕዝቦችን ነው። አ.ት፡ “የእነዚህ ነገዶች ሕዝቦች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የገሪዛን ተራራ

x

Deuteronomy 27:13

የጌባል ተራራ

ይህንን በዘዳግም 11፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

እርግማኖቹን ያውጁ

“እግዚአብሔር እስራኤልን እንዴት እንደሚረግማቸው በታላቅ ድምፅ ተናገር”

Deuteronomy 27:15

በድብቅ የሚያቆም ያ ሰው የተረገመ ይሁን

ይህ ሌዋዊው ለእስራኤል ሕዝብ በሙሉ ጮክ ብሎ የሚያደርገው ንግግር ነው። ይህ ንግግር በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በድብቅ የሚያቆመውን ሰው እግዚአብሔር ይርገመው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የባለሙያ እጅ የሠራውን

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ሰው የሠራው አንድ ነገር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ባለሙያ

ነገሮችን ጥሩ አድርጎ መሥራት የሚያውቅ ሰው

Deuteronomy 27:16

ሰውየው የተረገመ ይሁን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሰውየውን ይርገመው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የባልንጀራውን የድንበር ምልክት የሚያስወግድ

የዚህ አነጋገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በመሬቱ ድንበር ላይ ያሉትን ምልክቶች በማንሣት ከባልንጀራው መሬት የሚወስድ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 27:18

ሰውየው የተረገመ ይሁን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 27፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሰውየውን ይርገመው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ለመጻተኛው፣ -- ለመበለቲቱ የሚገባውን ፍትሕ ጉልበቱን ተጠቅሞ የሚነጥቅ

ሙሴ ስለ ፍትሕ የሚናገረው አንድ ጉልበተኛ የሆነ ሰው ደካማ ከሆነው ሰው ላይ በኃይል እንደሚቀማው አካላዊ ቁስ አድርጎ ነው። የአንተ ቋንቋ ምናልባት “ጉልበቱን ተጠቅሞ የሚነጥቅ” ለማለት የሚያስችል አንድ ቃል ይኖረው ይሆናል። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 24፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “መጻተኛውን -- መበለቲቱን የሚበድል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አባቶቻቸውን ያጡ ልጆች

እነዚህ ሁለቱም ወላጆቻቸው የሞቱባቸውና የሚንከባከባቸው ዘመድ የሌላቸው ልጆች ናቸው።

Deuteronomy 27:20

ሰውየው የተረገመ ይሁን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 27፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሰውየውን ይርገመው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የአባቱን ሚስት

ይህ የአባቱን ሌላኛዋን ሚስት እንጂ የሰውየውን እናት አያመለክትም።

የአባቱን መብት ወስዷል

አንድ ሰው ሚስት በሚያገባበት ጊዜ እርሱ ብቻ ከእርሷ ጋር የመተኛት ሕጋዊ መብት ይኖረዋል። የዚህ አነጋገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የአባቱን ሕጋዊ መብት ወስዶበታል” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

ከየትኛውም ዓይነት እንስሳ ጋር የሚተኛ

የዚህ አነጋገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከየትኛውም ዓይነት እንስሳ ጋር የሚተኛ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 27:22

ሰውየው የተረገመ ይሁን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 27፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሰውየውን ይርገመው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከአባቱ ሴት ልጅ ወይም ከእናቱ ሴት ልጅ ጋር

ይህ ማለት አንድ ሰው ከሌላ እናት ወይም አባት ብትወለድም እንኳን ከእህቱ ጋር ሊተኛ አይችልም።

Deuteronomy 27:24

ሰውየው የተረገመ ይሁን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 27፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሰውየውን ይርገመው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 27:26

ሰውየው የተረገመ ይሁን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 27፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሰውየውን ይርገመው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 28

1 ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ በፍጹም ብትታዘዙና እኔ ዛሬ የምሰጣችሁን ትእዛዘትን ሁሉ በጥንቃቄ ብትከተሉ አምላካችሁ እግዝአብሔር በምድር ላይ ከሚኖሩ አሕዝብ ሁሉ በላይ ከፍ ያደርጋችኋል። 2 እግዚአብሔር አምላካችሁን ብትታዘዙ እነዚህ በረከቶች ሁሉ የእናንተ ይሆናሉ፤ አይለዩአችሁምም። 3 በከተማና በእርሻ ትባረካላችሁ። 4 የማሕፀናችሁ ፍሬ፥ የምድራችሁ አዝመራ፥ የእንስሳታችሁ ግልገሎች፥ የክብታችሁ ጥጃ፥ የበግና የፍየል ግልገሎቻችሁም ይባረካሉ። 5 እንቅባችሁና ቡሓቃያችሁም ይባረካሉ። 6 ስትጓዙ ትበረካላችሁ፤ ስትወጡም ትባረካላችሁ። 7 እግዚአብሔር በእናንተ ላይ የሚነሡ ጠላቶቻችሁን በፊታችሁ እንዲሸነፉ ያደርጋቸዋል፤በአንድ አቅጣጫ ቢመጡባችሁ በሰባት አቅጣጫም ከእናንተ ይሸሻሉ። 8 እግዚአብሔር በጎተራችሁና እጃችሁ በነካው ሁሉ በረከቱን ይልካል። አምላካችሁ እግዚአብሔር በሚሰጣችሁ ምድር ላይ ይባርካችኋል። 9 የእግዚአብሔር የአምላካችሁ ትእዛዞች የምትጠብቁና በመንገዱ የምትሄዱ ከሆነ በማለላቸው ተስፋ መሠረት የተቀደሰ ሕዝቡ አድርጎ ያቆማችኋል። 10 ከዚያ የምድር አሕዝብ ሁሉ በእግዚአብሔር ስም መጠራታችሁን ያያሉ፤ ይፈርሁማል። 11 እግዚአብሔርም ሊሰጣችሁ ለአባቶቻችሁ በማለላቸው ምድር የማሕፀናችሁ ፍሬ፥ በእንስሳታችሁ፥ ግልገል፥ በምድራችሁም ሰብል፥ የተትረፈረፈ ብልጽግና ይሰጣችኋል። 12 እግአብሔር ለምድራችሁ በወቅቱ ዝናብን ለመስጠትና የእጃችሁን ሥራ ሁሉ ለመባረክ መልካሙን መዝገብ ሰማዩን ይከፍትላችኋል፤ እናንተም ለብዙ አሕዛብ ታበድራላችሁ እንጂ ከአንዳቸውም አትበደሩም። 13 እግዚአብሔም ራስ እንጂ ድራት አያደርጋችሁም፤ ዛሬ የምሰጣችሁን የአምላካችሁ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በጥንቃቄ ብትጠብቁ መቼውንም ቢሆን በላይ እንጂ ፈጽሞ በታች አትሆኑም። 14 ሌሎች አማልክት በመከተል እነርሱን በማገልገል ዛሬ ከምሰጣችሁ ትእዛዞች ቀኝም ግራም አትበሉ። 15 ነገር ግን ለእግዚአብሔር ለአምላካችሁ ባትታዘዙ በዛሬዋ ዕለት የምሰጣችሁን ትእዛዙንና ሥርዓቱን ሁል በጥንቃቄ ባትከተሉአቸው እነዚህ ርግማኖች ሁሉ ይደርሱባችኋል፤ ያጥለቀልቁአችኋልም። 16 በከተማ ትረገማላችሁ፤ በእርሻም ትረገማላችሁ። 17 እንቅባችሁና ቡሓቃያችሁ የተረገሙ ይሆናሉ። 18 የማሕፀናችሁ ፍሬ፥ የእርሻህ ሰብል፥ የመንጋችሁ ጥጆች፥ የበግና የፍየል ግልገሎቻችሁ ይረገማሉ። 19 ስትገቡ ትረገማላችሁ፤ ስትወጡም ትረገማላችሁ። 20 እርሱን በመተው ክፉ ድርጊት ከመፈለጋችሁ የተነሣ እስክትደመስሱ ፈጥናችሁም እስክትጠፉ ድረስ እጃችሁ በነካው ሁሉ ላይ እግዚአብሔር ርግማንን መደናገርንና ተግሣጽን ይሰድባችኋል። 21 እግዚአብሔር ልትወርሱአት ከምትገቡባት ምድር ላይ እስኪያጠፋችሁ ድረስም በደዌ ይቀሥፋችኋል። 22 እግዚአብሔር እስክትጠፉ ድረስ በሚቀሥፍ ደዌ ትኩሳትና ዕባጭ ኃይለኛ ሙቀትና ድርቅ ዋግና አረማሞ ይመታችኋል። 23 ከራሳችሁ በላይ ያለው ሰማይ ናስ ከእግራችሁ በታች ያለው ምድርም ብረት ይሆናል። 24 እግዚአብሔር የምድራችሁን ዝናብ ወደ አቧራነትና ወደ ትቢያነት ይለወጠዋል፤ ይህም እስክትጠፉ ድረስ ከሰማይ ይወርድባችኋል። 25 እግዚአብሔር በጠላቶቻችሁ ፊት እንድትሸነፉ ያደርጋችኋል፤ በአንድ አቅጣጫ ትመጣበቸዋላችሁ ነገር ግን በሰባት አቅጣጫ ከፊታቸው ትሽሻላችሁ ለምድር መንግሥታትም ሁሉ መሸማቀያ ትሆናላችሁ። 26 ሬሳችሁ ለሰማይ አሞሮችና ለምድር አራዊት ሲሳይ ይሆናል፤ በማስፈራራትም የሚያባርሩአቸው አይኖርም። 27 እግዚአብሔር በማትድኑበት በግብፅ ብጉጅ፥ በእባጭ በሚመግል ቁስልና በእከክ ያሠቃያችኋል። 28 እግዚአብሔር በእብደት፥ በዕውርነትና ግራ በማጋባት ያስጨንኣቃችል። 29 በእኩለ ቀን በጨለማ እንዳለ ዕውር በዳበሳ ትሄዳላችሁ። የምታደርጉት ሁሉ አይሳካላችሁም። በየዕለቱ ትጨቆናላችሁ፤ ትመዘበራላችሁም፤ የሚታደጋችሁም አይኖርም። 30 ሚስት ለማግባት ልጃገረድ ታጫላችሁ ሌላው ግን ወስዶ በኃይል ይደፍራታል። ቤት ትሠራላችሁ፤ ግን እናንተ አትኖሩበትም። ወይን ትተክላላችሁ ፍሬውን ግን አትበሉም። 31 በሬህ ዐይናችሁ እያየ ይታረዳል፤ ከሥጋውም አንዳች አትቀምሱም። አህያችሁም በግድ ይወሰድባችኋል፤ አትበሉም። በጎቻችሁ ለጠላቶቻችሁ ይሰጣሉ፤ የሚያሰጥላቸውም አይኖርም። 32 ወዶችና ሴቶች ልጆቻችሁ ለባዕድ ሕብብ ይሰጣሉ፤ እጃችሁንም ለማንሣት እቅም ታጣላችሁ፤ ይመጣሉ፤ በማለትም ዐይኖቻችሁ ሁልጊዜ እነርሱን በመጠባበቅ ይደክማሉ። 33 የምድራችሁንና የድካማሁን ፍሬ ሁሉ የማታውቁት ሕዝብ ይበላዋል፤ 34 ሁልጊዜ በጭቆናና በጫን ትኖራላችሁ፤ በምታዩት ሁሉ ትጃጀላላችሁ። 35 እግዚአብሔር ከእግራችሁ ጥፍር እስከ ራስህ ጠጉር በሚወርር ሊድን በማይችልና በሚያሠቃይ ቁስል ጉልበታችሁንና እግራችሁን ይመታችኋል። 36 እግዚአብሔር እናንተንና በላያችሁ ያነገሣችሁትን ንጉሥ፥ እናንተና አባቶቻችሁ ወደ ማታውቁት ሕዝብ ይወሰዳችኋል፤ ከዚያም ከእንጨትና ከድንጋይ የተሠሩ ሌሎች አማክልትን ታመልካላችሁ። 37 እግእብብሔር እንድትገቡ በሚመራችሁ ምድር ለአሕዛብ ሁሉ መሸማቀቂያ ማላገጫና መዘባበቻ ትሆናላችሁ። 38 በእርሻ ላይ ብዙ ዘር ትዘራላችሁ አንበጣ ስለሚበላው የምትሰበስቡ ጥቂት ይሆናል። ወይን ትተክላላችሁ ትንከባከበዋላችሁ፤ 39 ነገር ግን የወይን ጠጁን አትጠጡም ዘለላውንም አትሰበስቡም። 40 በአገራችሁ ምድር ሁሉ የወይራ ዛፍ ይኖራችኋል፤ ፍሬው ስለሚረግፍባችሁ ግን ዘይቱን አትቀቡም። 41 ወንዶችንና ሴቶች ልጆቻችሁን ትወልዳላችሁ ነገር ግን በምርኮ ስለሚወሰዱ፤ አብረዋችሁ አይኖሩም። 42 ዛፋችሁንና የምድራችሁን ሰብል ሁሉ አንበጣ መንጋ ይወረዋል። 43 በመካከላችሁ የሚኖር መጻተኛ ከእናንተ በላይ ከፍ ከፍ ሲል እናንተ ግን ዝቅ ዝቅ ትላላችሁ። 44 እርሱ ያበድራችኋል እንጂ እናንተ አታበድሩም። እርሱ ራስ ይሆናል፤ እናንተ ግን ጅራት ትሆናላችሁ። 45 እነዚህ ርግማኖች እስክትጠፉ ድረስ ይከተሉአችኋል፤ ሁሉ በእናንተ ላይ ይመጣሉ፤ ይህም የሚሆነው አምላካችሁን እግዚአብሔርን ስላልታዘዛችሁና የሰጣኋችሁን ትእዛዝና ሥርዓት ስላልጠበቃችሁ ይወርዱባችኋልም። 46 እነዚህ ርግማኖች እንደ ምልክትና ድንቅ ነገሮች ሆነው በእንንተና በዘራችሁ ለዘላለም ይሆናል። 47 በብልጽግና ጊዜ እግዚአብሔር አምላካችሁን በደስታና በሐሤት ስላላገለገችሁ በራብና በጥም በእርዛትና በከፋ ድኽነት 48 እግዚአብሔር የሚያስነሣባችሁን ጠላቶቻችሁን ታገለግላላችሁ፤ እስኪያጠፉአችም ድረስ በአንገታችሁ ላይ የብረት ቀንበር ይጭንባችኃል። 49 እግዚአብሔር እንደ ንስር በፈጣን የሚበሩና ቋንቋውን የማታውቁአችሁን ሕዝብ እጅግ ሩቅ ከሆነ፥ ከምድርም ዳርቻ ያስነሣነሰባችኋል፤ 50 ሽማግሌ የማያከብር፥ ለወጣትም መልካም ያልሆኑና የሚያስፈራና ጨካኝ ሕዝብ ነው። 51 እስክትጠፉም ድረስ የእንስሳታችሁን ግልገልና የምድራችሁን ሰብል ይበላል፤ እስኪያጠፋችሁም ድረስ እህል፤አዲስ የወይን ጠጅና ዘይት የመንጋችሁን ጥጃና የበግና ፍየል መንጋችሁን ግልገል አያስቀሩላችሁም። 52 የምትታመኑባቸውን ታላላቅ የተመሸጉ ቅጥሮች እስኪወድቁ ድረስ በመላው አገራችሁ ያሉትን ከተሞቻችሁን ሁሉ ይከባል፤ አምላካችሁ እግዚአብሔር በሚሰጥጣችሁምድር ያሉትን ከተሞች በሙሉ ይወራቸዋል። 53 ጠላቶቻችሁ ከበው በሚያስጨንቁአችሁ ጊዜ ከሥቃይ የተነሣ አምላካችሁ እግዚአብሔር የሰጣችህን የአብራካችሁ ፍሬ የሆኑትን የወንዶችና የሴቶች ልጆቻችሁን ሥጋ ትበላላችሁ። 54 ሌላው ይቅርና በመካከላችሁ በጣም ደግና ርኅሩኅ የሆነው ሰው እንኳ ለገዛ ወንድሙ ወይም ለሚወዳት ሚስቱ ወይም ለተረፉት ልጆቹ አይራራላቸውም። 55 ከሚበላው ከልጆቹ ሥጋ ላይም ቅንጣት ያህል እንኳ ከእነርሱ ለአንዱ አያቀምስም፤ ከተሞቻችሁ ሁሉ በመከበባቸው ጠላቶቻችሁ ከሚያደርሱባችሁ ሥቃይ የተነሣ ለእርሱ የቀረለት ይህ ብቻ ነውና። 56 በመካከላችሁ ተመቻችታና ተቀማጥላ የምትኖር ከልስላሴና ከቅምጥልነት የተነሣ እግሯን አፈር ነክቶት የማያውቅ ሴት የምትወደውን ባሏን፥ የገዛ ወንድና ሴት ልጆቿን ትንቃለች። 57 ከማሕፀኗ የወጣውን የምትወልዳቸውን ሕፃናት ትጠየፋለች፤ በመከራው ወቅት ጠላቶቻችሁ ከተሞቻችሁን ከበው በሚያስጨንቁአችሁ ጊዜ ሌላ የሚበላ ስለማይኖር እነርሱን ደብቃ ትበላለች። 58 በዚህ መጽሐፍ የተጻፉትን የዚህን ሕግ ቃሎች ባትከተሉና የተከበረውና አስፈሪ የሆነውን የአምላካችሁን 59 የእግዚአብሔርን ስም ባታከብሩ እግዚአብሔር አስፈሪ መቅሠፍት፥ አስጨናቂና ለብዙ ጊዜ የሚቋይ መዓት አሠቃቂና በቀላሉ የማይወገድ ደዌ በእናንተና በዘሮቻችሁ ላይ ይልክባችኋል። 60 የምትፈሩአችሁንም የግብፅ በሽታዎች ሁሉ ያመጣባችኋል፤ በእናንተም ላይ ይጣበቃሉ። 61 ደግሞም እግዚአብሔር በዚህ የሕግ መጽሐፍ ያልተጸፈውን ማንኛውንም ዓይነት ደዌና መከራ እስክትጠፉ ድረስ ያመጣባችኋል። 62 ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር ስላልታዛዝችሁ እንደ ሰማይ ከዋክብት በዝታችሁ ቢሆን እንኳ እናንተ ጥቂት ብቻ ትቀራላችሁ። 63 እግዚአብሔር ለእናንተ መልካም በማድረግና ቁጥራችሁን በማብዛት ደስ እንዳተሰኘ ሁሉ ፤ እናንተን በመደምሰስና በማጥፋት ደስ ይለዋል። ከምትወርሱዋት ምድር ትነቀላላችሁ። 64 ከዚያም እግዚአብሔር ከአንዱ የምድር ዳርቻ እስከ ሌላው ዳርቻ በሕዝቦች ሁሉ መካከል ይበትናችኋል። በዚያም አባቶአኣችሁ የማታውቋቸውን ከእንጨትና ከድንጋይ የተሠሩ ሌሎች አማልክትን ታመልካላችሁ። 65 በእነዚያ ሕዝቦች መካከል ዕረፍት አታገኙም፤ ለእግራችሁም ጫማ ማረገጫ አይኖርም፤ እዚያም እግዚአብሔር የሚጨነቅ አእምሮ፥ የሚደክም ዐይንና ተስፋ የሚቋርጥ ልብ ይሰጣችኋል። 66 ዘመናችሁን በሙሉ ቀንና ሌሊት በፍርሃት እንደ ተዋጣችሁ ሕይወትታችሁ ዘወትር በሥጋት ትኖራላችሁ። 67 ልባችሁ በፍርሃት ከመሞላቱና ዐይናችሁ ከሚያየው ነገር የተነሣ ሲነጋ ምነው አሁን ሲመሽ ፥ደግሞ ምነው አሁን በነጋ ትላላችሁ። 68 ዳግመኛ አትመለሱባትም ባልሁ መንገድም እግዚአብሔር በመርከብ ወደ ግብፅ ይመልሳችኋል። እዚያም እንደ ወንድና ሴት ባሪያ ለጠላቶቻችሁ ለመሸጥ ራሳችሁን ታቀርባላችሁ የሚገዛችሁ ግን አይኖርም።



Deuteronomy 28:1

ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ድምፅ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው እርሱ የሚናገረውን ነው። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር ለሚናገረው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ትጠብቀው ዘንድ

“ትታዘዘው ዘንድ”

ከላይ ያደርግሃል

ሙሴ ከፍ ባለ ኮረብታ ላይ በአካል ከፍ እንደ ማለት አስፈላጊ ስለ መሆን ወይም ታላቅ ስለ መሆን ይናገራል። አ.ት፡ “ከ -- ይልቅ በጣም አስፈላጊ ያደርግሃል” ወይም “ከ-- ይልቅ ታላቅ ያደርግሃል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እነዚህ በረከቶች ሁሉ ይመጡብሃል፣ ይደርሱብሃልም

ሙሴ በረከቶችን የሚገልጻቸው በድንገት እንደሚያጠቃቸው ወይም አሳዶ እንደሚይዛቸው ሰው አድርጎ ነው። አ.ት፡ “ፈጽሞ በምትገረምበት እንዲህ ባለ መንገድ እግዚአብሔር ይባርክሃል፣ ይኸውም ልታመልጥ በማትችልበት መልኩ ይባርክሃል” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:3

ትባረካለህ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ይባርክሃል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በከተማ - በእርሻ

ይህ ቁንጽል፣ እግዚአብሔር በሁሉም ስፍራ ይባርካቸዋል የሚል ትርጉም አለው። (See: Merism)

የአካልህ ፍሬ፣ የመሬትህ ፍሬ፣ የእንስሳህ ፍሬ

“ልጆችህ፣ ሰብልህ፣ እና እንስሶችህ” እነዚህ የአነጋገር ዘይቤዎች እስራኤላውያን ዋጋ ለሚሰጧቸው ነገሮች በሙሉ በቁንጽል አመልካቾች ናቸው። (የአነጋገር ዘይቤ እና Merism የሚለውን ተመልከት)

የእንስሳህ ፍሬ፣ የከብቶችህ ፍሬ፣ እና የበግና የፍየል ጠቦቶችህ

ይህ ጥምረት እግዚአብሔር የእስራኤላውያንን እንስሶች እንደሚያበዛቸውና እንደሚያበረታቸው በሦስት መንገድ መናገሪያ ነው። አ.ት፡ “የከብቶቻችሁ ጥጃዎች እና የበግና የፍየል መንጋ ጠቦቶቻችሁ ከእንስሶቻችሁ ሁሉ ጋር” (See: Doublet)

Deuteronomy 28:5

ይባረካሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ይባርካል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ቅርጫትህና ቡሓቃህ

እስራኤላውያን ቅርጫትን ጥራጥሬ ለመሸከም ይጠቀሙበት ነበር። “ቡሓቃ” እንጀራ ለመጋገር ዱቄቱን የሚያዋህዱበት ጎድጎድ ያለ ዕቃ ነው። አ.ት፡ “የምታበቅለው እህል እና የምትበላው ምግብ ሁሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በምትገባበት ጊዜ -- በምትወጣበት ጊዜ

ይህ ጥምረት በሚሄዱበት ቦታ ሁሉ የሚኖራቸውን የሕይወት ተግባራት በሙሉ ያመለክታል። (See: Merism)

Deuteronomy 28:7

በላይህ ላይ የተነሣውን ጠላትህን በፊትህ ተመትቶ እንዲወድቅ ያደርገዋል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሚዋጉህን ጠላቶችህን እንድታሸንፋቸው ያደርግሃል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሆኖም በሰባት መንገድ ከአንተ ይሸሻሉ

“ሆኖም በሰባት አቅጣጫ ከአንተ በሩጫ ይሸሻሉ”

ሰባት መንገድ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ትክክለኛው ቁጥር ከሰባት ሊበልጥ ወይም ሊያንስ ይችላል። አ.ት፡ “በብዙ የተለያዩ አቅጣጫዎች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በረከት በጎተራህ እንዲመጣ እግዚአብሔር ያዘዋል

እግዚአብሔር አንድ ሰው በድንገት እስራኤላውያንን እንዲያጠቃቸው የሚያዝ በሚመስል መልኩ እግዚአብሔር እንደሚባርካቸው ሙሴ ያብራራል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በሚባርክህ ጊዜ በጎተራህ ባለው ጥራጥሬ ብዛት ትገረማለህ” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

እጅህን በምታኖርበት ሁሉ ላይ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በምትሠራው ነገር ሁሉ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:9

እግዚአብሔር ለራሱ የተለየ ሕዝብ አድርጎ ያቆምሃል

እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ የራሱ እንዲሆን በተለየ ሁኔታ መምረጡ ሌሎች ሕዝቦች በሙሉ ከሚኖሩበት ስፍራ ልዩ በሆነ ቦታ እግዚአብሔር እንዳስቀመጣቸው ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ለእርሱ የሚሆን ቅዱስ ሕዝብ ያደርግሃል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእግዚአብሔር ስም ተጠርተሃል

እዚህ ጋ “በእግዚአብሔር ስም ተጠርተሃል” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ትርጉም የእርሱ መሆን ማለት ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የራሱ አድርጎ ጠርቶሃል” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:11

በአካልህ ፍሬ፣ በከብቶችህ ፍሬ፣ በመሬትህ ፍሬ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 28፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “በልጆች፣ እንስሳትና ሰብል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከሰማይ መጋዘኑ

ሙሴ ዝናቡን የሚያስቀምጥባቸው ሕንጻዎች በሚመስሉበት መልኩ ዝናብ ስለሚያዘንቡ ደመናት ይናገራል። አ.ት፡ “ደመናት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በትክክለኛው ጊዜ

“ሰብሎች በሚፈልጉት ጊዜ”

የእጆችህ ሥራ ሁሉ

“እጅ” የሚለው ቃል የሙሉው ሰው ተምሳሌት ነው። አ.ት፡ “የምትሠራው ሥራ ሁሉ” (See: Synec- doche)

Deuteronomy 28:13

ራስ እንጂ ጅራት አትሆንም

ይህ ዘይቤአዊ አነጋገር የእስራኤልን ሕዝብ እንደ እንስሳ ይገልጸዋል፣ ይኸውም እስራኤላውያን ሁልጊዜ የሌሎች ሕዝቦች መሪዎች ይሆናሉ እንጂ ከቶም አገልጋዮቻቸው ለመሆን ከኋላ አይከተሉም ማለት ነው። እስራኤላውያን በኃይል፣ በገንዘብና በክብር ብልጫ ያላቸው ይሆናሉ። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከላይ ብቻ ይሆናሉ -- ፈጽሞ ከበታች አይሆኑም

እስራኤላውያን በሌሎች ላይ ገዢዎች ይሆናሉ እንጂ ሌሎች አይገዟቸውም።

እኔ አዛችኋለሁ

ሙሴ የሚናገረው ለእስራኤላውያን በሙሉ ነው፣ ስለዚህ “አንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

እኔ ዛሬ ከማዝህ ቃል ሁሉ ሌሎች አማልክትን ተከትለህ ለማገልገል ወደ ቀኝ ወይም ወደ ግራ ካልተከተልክ

እግዚአብሔርን አለመታዘዝና ሌሎች አማልክትን ማምለክ ልክ አንድ ሰው በአካሉ ከእግዚአብሔር ቃል ተመልሶ በሌላ አቅጣጫ እንደ ሄደ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ሌሎች አማልክትን በማገልገል ዛሬ እኔ የማዝህን ባትታዘዝ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:15

ነገር ግን ባትታዘዝ

እዚህ ጋ ሙሴ ሕዝቡ ባይታዘዙ የሚደርስባቸውን እርግማን መዘርዘር ይጀምራል።

የአምላክህ የእግዚአብሔር ድምፅ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ትርጉሙ እግዚአብሔር የሚናገረው ማለት ነው። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር የሚናገረው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከዚያም እነዚህ እርግማኖች ሁሉ ይመጡብሃል፣ ይደርሱብሃል

ሙሴ እርግማኖቹን የሚገልጻቸው በድንገት እንደሚያጠቃቸው ወይም አሳዶ እንደሚይዛቸው ሰው አድርጎ ነው። አ.ት፡ “ፈጽሞ በምትደነቅበት ሁኔታ እግዚአብሔር ይረግምሃል፣ ይህም አንተን ከሚረግምበት ከእርግማኑ ማምለጥ በማትችሉበት ሁኔታ ነ፞ው” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

ይመጡብሃል፣ ይደርሱብሃል

ይህንን በዘዳግም 28፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 28:16

የተረገምክ ትሆናለህ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ይረግምሃል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በከተማ -- በእርሻ

የዚህ ጥምረት ትርጉም እግዚአብሔር በሁሉም ስፍራ ይባርካቸዋል የሚል ነው። ይህንን በዘዳግም 28፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (See: Merism)

ቅርጫትህና ቡሓቃህ

እስራኤላውያን ቅርጫትን ጥራጥሬ ለመሸከም ይጠቀሙበት ነበር። “ቡሓቃ” እንጀራ ለመጋገር ዱቄቱን የሚያዋህዱበት ጎድጎድ ያለ ዕቃ ነው። ይህንን በዘዳግም 28፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “የምታበቅለው እህል እና የምትበላው ምግብ ሁሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:18

የተረገመ ይሆናል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ይረግማል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የአካልህን ፍሬ፣ የመሬትህን ፍሬ

ይህ “ልጆችህ፣ ሰብልህ” ለሚለው የአነጋገር ዘይቤ ነው። ይህንን በዘዳግም 28፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የከብትህ፣ የበግና የፍየል ጠቦቶችህ ብዛት

ይህ ጥምረት እግዚአብሔር የእስራኤላውያንን እንስሳ ብዙና ብርቱ እንደሚያደርጋቸው በሁለት መንገድ የተነገረበት ነው። አ.ት፡ “የከብቶቹ ጥጃዎች፣ የበግና የፍየል መንጋው ጠቦቶች” (See: Doublet)

በምትገባበት ጊዜ -- በምትወጣበት ጊዜ

ይህ ጥምረት የሚያመለክተው በሚሄዱበት ቦታ ሁሉ የሚሆነውን የሕይወት ተግባራት በሙሉ ነው። ይህንን በዘዳግም 28፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (See: Merism)

Deuteronomy 28:20

እርግማን፣ መደናገር፣ እና ተግሳጽ

“እልቂት፣ ፍርሀት እና መሳቀቅ”

እጅህን በምታኖርበት ሁሉ ላይ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በምትሠራው ነገር ሁሉ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እስክትጠፋ ድረስ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ጠላቶችህ እስኪያጠፉህ ድረስ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ይጣበቅብሃል

“በአንተ ላይ ይኖራል”

እኔን ትተኸኛል

እዚህ ጋ “እኔን” የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ነው።

ይጣበቅብሃል

“በአንተ ላይ ይኖራል”

Deuteronomy 28:22

ተላላፊ በሽታ፣ ትኩሳት፣ በሰውነት መመረዝ

“በሽታና የሚያቃጥል ትኩሳት ያደክምሃል”። እነዚህ ሁሉ የሚያመለክቱት ሰዎች እንዲዳከሙና እንዲሞቱ የሚያደርጋቸውን በሽታ ነው።

በድርቅ

“በዝናብ እጥረት”

ዋግ

በሰብል ላይ የሚበቅል ሻጋታ ሲሆን እንዲበሰብሱ ያደርጋቸዋል

እነዚህ ያሳድዱሃል

ሙሴ በእስራኤላውያን ላይ ስለሚደርስባቸው ክፉ ነገሮች ሲናገር ከእስራኤላውያን በስተኋላ ሆነው በሚያሳድዱ ሰዎች ወይም እንስሶች አስመስሎ ይናገራል። አ.ት፡ “በእነርሱ ምክንያት ትሰቃያለህ” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:23

ሰማይ ናስ ይሆናል

ሙሴ ዝናብ ስለማይኖር ሰማዩ እንደ ናስ እንደሚሆን ይናገራል። አ.ት፡ “ሰማይ -- ዝናብን አይሰጥም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ምድር -- ብረት ትሆናለች

ሙሴ ምድር ምንም ሰብል ስለማይበቅልባት እንደ ብረት እንደምትሆን ይናገራል። አ.ት፡ “መሬቱ ላይ ምንም ነገር አይበቅልም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የምድርህን ዝናብ እግዚአብሔር ወደ ትቢያና አቧራ ይለውጠዋል

“እግዚአብሔር በዝናብ ምትክ አሸዋ አዘል ውሽንፍር ይልካል”

እስክትጠፋ ድረስ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እስኪያጠፋህ ድረስ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:25

እግዚአብሔር በጠላቶችህ ፊት ተመትተህ እንድትወድቅ ያደርግሃል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ጠላቶችህን መትተው እንዲጥሉህ ያደርጋቸዋል”

በ -- ፊት ተመትተህ እንድትወድቅ

ይህንን በዘዳግም 28፡7 ላይ እንዴት እንደተረግምከው ተመልከት።

በሰባት መንገድ ከእነርሱ ትሸሻለህ

ይህ ማለት እስራኤላውያን ፈርተውና ደንግጠው ከጠላቶቻቸው ይሸሻሉ። የቃላቶቹን ተመሳሳይነት በዘዳግም 28፡7 ውስጥ ተመልከት። (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሰባት መንገዶች

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በብዙ የተለያዩ አቅጣጫዎች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በመንግሥታት ሁሉ መካከል ትቅበዘበዛለህ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሌሎች ሀገራት ሰዎች ከአንዱ ሕዝብ ወደ ሌላው ያባርሯችኋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:27

የግብፅን ዕባጭ

“ግብፃውያንን በረገምኩበት በዚያው የቆዳ በሽታ”

ዕባጭ -- የቆላ ቁስል፣ የደም በሽታና እከክ

እነዚህ ልዩ ልዩ ዓይነት የቆዳ በሽታዎች ናቸው።

ልትድን የማትችልበትን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማንም ሊፈውስህ የማይችለውን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ዐይነ ሥውር በጨለማ በዳበሳ እንደሚሄድ በእኩለ ቀን በዳበሳ ትሄዳለህ

“በእኩለ ቀን እንኳን በዳበሳ እንደሚሄዱ እንደ ዐይነ ሥውራን ትሆናለህ”። እያንዳንዱ በሕይወቱ በሚደሰትበት ጊዜ እንኳን እስራኤላውያን አስቸጋሪ ሕይወት ይኖራቸዋል። (See: Simile)

ሁልጊዜ የተጨቆንክና የተዘረፍክ ትሆናለህ

“የበረቱ ሕዝቦች ሁልጊዜ ይጨቁኑሃል፣ ይዘርፉሃልም”

Deuteronomy 28:30

በዐይንህ ፊት በሬህ ይታረዳል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው በሬህን ሲያርደው ታያለህ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በፊትህ አህያህ በግድ ይወሰድብሃል፣ አይመለስልህም

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው አህያህን በጉልበት ይወስድብሃል፣ አይመልስልህምም” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በጎችህ ለጠላቶችህ ይሰጣሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በጎችህን ለጠላቶችህ እሰጣቸዋለሁ” ወይም “ጠላቶችህ በጎችህን እንዲወስዱ እፈቅድላቸዋለሁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:32

ወንዶችና ሴቶች ልጆች ለሌሎች ሕዝቦች ይሰጣሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ወንዶችና ሴቶች ልጆችህን ለሌሎች ሕዝቦች እሰጣቸዋለሁ” ወይም “ጠላቶችህ ወንዶችና ሴቶች ልጆችህን ይወስዷቸዋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ዐይኖችህ ቀኑን ሙሉ እነርሱን ይጠባበቃሉ፣ ሆኖም እነርሱን በመናፈቅ ይዝላሉ

እዚህ ጋ “ዐይኖችህ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “እነርሱን በመጠባበቅና ዳግመኛ ልታያቸው በመናፈቅ ትደክማለህ” (See: Synecdoche)

ምንም ብርታት በእጅህ ላይ አይኖርህም

እዚህ ጋ “ብርታት በእጅህ ላይ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው ኃይልን ነው። አ.ት፡ “ስለጉዳዩ አንዳች ለማድረግ ኃይል አይኖርህም” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:33

ሀገር

እዚህ ጋ “ሀገር” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሀገሩ ሕዝብ ማለት ነው። አ.ት፡ “የሀገሩ ሕዝብ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሁልጊዜ የተጨቆንክና የተረገጥክ ትሆናለህ

“የተጨቆንክ” እና “የተረገጥክ” የሚሉት ቃላት መሠረታዊ ትርጉማቸው አንድ ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሁልጊዜ ይጨቁኗችኋል፣ ይረግጧችኋልም” ወይም “ባለማቋረጥ ይጨቁኗችኋል” (Doublet እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የሚሆነውን በማየት ታብዳለህ

“የምታየው እንድታብድ ያደርግሃል”

ልትድን በማትችልበት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማንም መፈወስ በማይችልበት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:36

እግዚአብሔር በሚወስድህ ሕዝቦች ሁሉ መካከል ጥላቻ፣ ምሳሌና መሳለቂያ

እዚህ ጋ “ምስሌ” እና “መሳለቂያ” የሚሉት ቃላት በመሠረቱ ትርጉማቸው አንድ ነው። ይህ እንደ አዲስ ዐረፍተ ነገር ተደርጎ መተርጎም ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በሚልክህ ስፍራ ሕዝቡ የጥላቻ፣ ስለ አንተም ምሳሌና መሳለቂያን ያደርጋል” ወይም “እግዚአብሔር ከጥላቻ የተነሣ ወደሚስቁብህና ወደሚቀልዱብህ ሕዝቦች ይልክሃል” (See: Doublet)

መሳለቂያ

ሰዎች ሌሎችን ለማሳፈር የሚጠቀሙበት ቃል ወይም ሐረግ

Deuteronomy 28:38

ነገር ግን ጥቂት ዘር ትሰበስባለህ

“ነገር ግን በጣም ጥቂት ምግብ ታከማቻለህ”

Deuteronomy 28:40

ነገር ግን ምንም ዘይት በራስህ ላይ አትቀባም

ሰዎች የቆዳቸውን ጤና ለመጠበቅ የወይራ ዘይት ይቀቡ ነበር።

የወይራ ዛፎችህ ፍሬአቸውን ያረግፋሉ

ፍሬው ከመብሰሉ በፊት እንደሚረግፍ ግልጽ ማድረግ ያስፈልግህ ይሆናል። አ.ት፡ “ፍሬው ከመብሰሉ በፊት የወይራ ዛፎችህ ፍሬአቸውን ያረግፋሉ” ወይም “የወይራው ፍሬዎች ከመብሰላቸው በፊት ከወይራ ዛፎችህ ላይ ይወድቃሉ” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 28:42

መጻተኛው -- እርሱ -- ለእርሱ

ይህ ማንነቱ የታወቀ መጻተኛ አይደለም፣ ነገር ግን በጥቅሉ መጻተኞችን ያመለክታል። አ.ት፡ “መጻተኞች የሆኑ -- እነርሱ -- ለእነርሱ” (See: Generic Noun Phrases)

ከአንተ በላይ ከፍ ከፍ ይላል፤ አንተ ራስህ ዝቅ ዝቅ እያልክ ትመጣለህ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ የሚለው ከእስራኤላውያን የበለጠ ኃይል፣ ገንዘብና ክብር መጻተኞች ይኖራቸዋል ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ ራስ ይሆናል፣ አንተ ጅራት ትሆናለህ

ይህ ማለት መጻተኞች ከእስራኤላውያን የበለጠ ኃይልና ሥልጣን ይኖራቸዋል። በዘዳግም 28፡13 ተመሳሳዩን ሐረግ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:45

እነዚህ እርግማኖች ሁሉ እስክትጠፋ ድረስ ይመጡብሃል፣ ያሳድዱሃል፣ ይደርሱብሃልም

ሙሴ እርግማኖችን በድንገት እንደሚያጠቃቸው ወይም አሳዶ እንደሚይዛቸው ሰው አድርጎ ይገልጻቸዋል። ተመሳሳዩን በዘዳግም 28፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እንደዚህ በሚያስገርምህ መንገድ ይረግምሃል፣ ይህም እንደሚያሳድድህና ሳይረግምህ በማታመልጠው ሁኔታ ይሆናል” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ድምፅ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” የሚሉት ቃላት እግዚአብሔር ለሚናገረው ፈሊጣዊ አነጋገሮች ናቸው። አ.ት፡ “አምላክህ እግዚአብሔር ለተናገረው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ትዕዛዙንና ሥርዓቱን

“ትዕዛዝ” እና “ሥርዓት” የሚሉት ቃላት “እግዚአብሔር እንድታደርገው ያዘዘህን ሁሉ” ለሚለው ጥምረት ናቸው። (See: Doublet)

Deuteronomy 28:47

በደስታና በልብ ሐሴት

እዚህ ጋ “በደስታ” እና “በልብ ሐሴት” ማለት ትርጉማቸው አንድ ነው። ሕዝቡ እግዚአብሔርን ለማምለክ እጅግ ደስ ይላቸው እንደነበረ አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Doublet)

በአንገትህ ላይ የብረት ቀንበር ያደርጋል

x

Deuteronomy 28:49

ከሩቅ፣ ከምድር ጥግ

ሁለቱም ሐረጎች ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆኑ ጠላት ከእስራኤል እጅግ ሩቅ ከሆነ ሀገር እንደሚመጡ አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Doublet)

ከምድር ጥግ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ስለ እርሱ ከማታውቀው ስፍራ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ንስር ወደ ግዳዩ እንደሚበር

ይህ ማለት ጠላት በድንገት ስለሚመጣ እስራኤላውያን ሊያስቆሟቸው አይችሉም። (See: Simile)

አዛውንቶችን የማያከብርና ርኅራኄ የሌለው፣ ቁጡ ፊት ያለው ሀገር

“ሀገር” የሚለው ቃል የዚያን ሀገር ሕዝብ የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ቁጡ ፊት ያለው፣ አዛውንቶችን የማያከብርና ርኅራኄ የሌለው ሕዝብ ሀገር”

እስክትጠፋ ድረስ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እስኪያጠፉህ ድረስ” ወይም “ምንም ነገር እስከማያስቀሩልህ ድረስ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:52

አንተን በከተማህ በሮች ሁሉ

እዚህ ጋ “የከተማ በሮች” የሚወክሉት ከተማን ነው። አ.ት፡ “ከተሞችህን” (See: Synecdoche)

የገዛ ሰውነትህን ፍሬ፣ የወንድና የሴት ልጆችህን ሥጋ

እዚህ ጋ “የወንድና የሴት ልጆችህን ሥጋ” የሚለው “የገዛ ሰውነትህን ፍሬ” የሚለውን ዘይቤአዊ አነጋገር ያብራራል። የጠላት ሰራዊት ከተማቸውን ከከበበ በኋላ ሕዝቡ የገዛ ልጆቻቸውን እስኪበሉ ድረስ ይራባሉ። (ዘይቤአዊ አነጋገር እና Parallelism የሚለውን ተመልከት)

የገዛ ሰውነትህን ፍሬ

ይህ የሚናገረው በወላጆቻቸው ሰውነት የተመረቱ ፍሬዎች በሚመስሉበት ሁኔታ ስለ ልጆች ነው። አ.ት፡ “የገዛ ራሳችሁ ልጆች” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:54

በመካከላችሁ ደግና በጣም ርኅሩኅ የሆነው እርሱ

“በመካከላችሁ ደግና በጣም ርኅሩኅ የሆነ ማነው? እርሱም እንኳን--”። ሙሴ የሚለው፣ አንድ ሰው ልጆቻቸውን ይበላሉ ብሎ የሚገምታቸው ብቻ ሳይሆኑ የመጨረሻዎቹ ይሆናሉ ብሎ የሚገምታቸውም እንኳን እነርሱ ልጆቻቸውን ይበላሉ።

የከተማህ በሮች ሁሉ

እዚህ ጋ “የከተማ በሮች” የሚወክሉት ከተሞቹን ራሳቸውን ነው። አ.ት፡ “ከተሞችህ በሙሉ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 28:56

በመካከላችሁ ደግና ርኅሩኅ የሆነች ሴት -- በደግነቷ -- እርሷ

x

Deuteronomy 28:58

የተጻፉትን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እኔ የጻፍኩትን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ይህ የአምላክህ የእግዚአብሔር ታላቅና አስፈሪ ስም

እዚህ ጋ “ስም” የተባለው ፈሊጣዊ አነጋገር ራሱን እግዚአብሔርን ያመለክታል። አ.ት፡ “ታላቅና አስፈሪ የሆነው አምላክህ እግዚአብሔር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር በአንተና በዘርህ ላይ አስከፊ መቅሠፍት ያደርግብሃል

“እግዚአብሔር በአንተና በዘርህ ላይ አስከፊ መቅሰፍት ይልካል” ወይም “እግዚአብሔር አንተንና ዘሮችህን በአስከፊ መቅሰፍቶች እንድትሰቃዩ ያደርጋል”

Deuteronomy 28:60

የግብፅን በሽታዎች ሁሉ በአንተ ላይ ያመጣል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንደገና በግብፅ በሽታዎች እንድትሰቃይ ያደርግሃል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በአንተ ላይ ይጣበቃሉ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በሽታዎቹ አያቆሙም፣ ደግሞም ማንም ከእነርሱ ሊያድንህ አይችልም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እያንዳንዱ ሕመምና ያልተጻፈ መቅሰፍት

እዚህ ጋ “እያንዳንዱ” በአጠቃላይ ሲሆን “ብዙ” ማለት ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እኔ ያልጻፍኳቸው ሌሎች ህመሞችና መቅሰፍቶች እንኳን” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት፣ አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እስክትጠፋ ድረስ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እስኪያጠፋህ ድረስ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ትቀራላችሁ -- እንደ -- የነበራችሁት -- አልሰማችሁም

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ ቡድን አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚልበት አገባብ ሁሉ ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

እንደ ሰማይ ከዋክበት ብዝታችሁ ነበር

ይህ ማለት ባለፈው ጊዜ ብዙ እስራኤላውያን ነበሩ። (See: Simile)

ለእግዚአብሔር ድምፅ

እዚህ ጋ “የእግዚአብሔር ድምፅ” የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር የሚያመለክተው እግዚአብሔር የሚናገረውን ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ለሚናገረው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:63

እግዚአብሔር በእናንተ ደስ ብሎት ነበር -- እናንተን በማብዛት -- እንድትደመሰሱና እንድትጠፉ በማድረግ በእናንተ ደስ ይለዋል። -- ትነቀላላችሁ።

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ ቡድን አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚልበት አገባብ ሁሉ ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

እግዚአብሔር ለእናንተ መልካም በማድረግና እናንተን በማብዛት ደስ ተሰኝቶባችሁ ነበር

“እግዚአብሔር ለእናንተ መልካም በማድረግና እንድትበዙ በማድረግ ተደስቶ ነበር"

እንድትደመሰሱ በማድረግ በእናንተ ደስ ይለዋል

“እንድትሞቱ በማድረግ ደስ ይለዋል”

ከምትወርሳት ምድር ትነቀላለህ

ሕዝቡ ፍራፍሬ የሆኑ ይመስል እግዚአብሔር እንደ ቁጥቋጦ እንደሚነቅላቸው ለመናገር ሙሴ ዘይቤአዊ አነጋገርን ይጠቀማል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ልትወርሱ ከምትገቡባት ምድር ያስወግዳችኋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በምትሄድበት -- ይበትንሃል -- ታመልካለህ -- የማታውቃቸውን -- አንተም ሆንክ አባቶችህ

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ ቡድን አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ እዚህ ጋ “አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት ቃላት ብዙ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

ከአንደኛው የምድር ጫፍ እስከ ሌላኛው የምድር ጫፍ

እነዚህ ሁለት ጽንፎች በአንድነት በምድር ላይ በሁሉም ስፍራ ማለት ነው። አ.ት፡ “በምድር ሁሉ” ወይም “በምድር ሁሉ ላይ” (See: Merism)

Deuteronomy 28:65

ለእግርህ መርገጫ እረፍት አይኖረውም

እዚህ ጋ “ለእግርህ መርገጫ” የሚለው ሐረግ የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “የምታርፍበት ቋሚ ቤት ስለማይኖርህ ባለማቋረጥ ትቅበዘበዛለህ” (See: Synecdoche)

በዚያ እግዚአብሔር የሚንቀጠቀጥ ልብ፣ የሚደክም ዐይንና የሚያለቅስ ነፍስ ይሰጥሃል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እንድትፈራ፣ ተስፋ እንዳይኖርህና እንድታዝን ያደርግሃል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሕይወትህ በፊትህ በጥርጣሬ ይንጠለጠላል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ትኖር ወይም ትሞት እንደሆነ አታውቅም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 28:67

በልብህ ካለው ፍርሀት የተነሣ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ከሚሰማህ ፍርሀት የተነሣ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ዐይኖችህ ከሚያዩአቸው ነገሮች የተነሣ

እዚህ ጋ “ዐይኖች” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “እንድታያቸው የማስገድድህን አስፈሪ ነገሮች” (See: Synecdoche and Assumed Knowledge and Implicit Information)

ተናግሬ ነበር

x


Chapter 29

1 እግዚአብሔር በኮሬብ ከገባው ቃል ኪዳን በተጨማሪ በሞዓብ ምድር ከእስራኤላውያን ጋር እንዲያደርግ ሙሴን ያዘዘው የኪዳኑ ቃሎች እነዚህ ናቸው። 2 ሙሴ እስራኤላውያንን ሁሉ ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ እግዚአብሔር በግብፅ በፈርዖን፥ በሹማምንቱ ሁሉና በመላ አገሩ ያደረተውን ሁሉ ዐይኖቻችሁ አይተዋል። 3 እነዚያን ከባድ ፈተናዎች ታምራዊ ምልክቶችና ታላቅ ድንቆች በገዛ ዐኖቻችሁ አይታችኋል። 4 ነገር ግን እስከ ዛሬ ድረስ እግዚአብሔር የሚያስተውል አእምሮ ወይም የሚያይ ዐይን ወይም የሚሰማ ጆሮ አልሰጣችሁም። 5 በምድረ በዳ በመራኋችሁ በእነዚያ አርባ ዓመታት ውስጥ ልብሳችሁ አላረጀም፥ የእግራችሁም ጫማ አላለቀም፥ 6 ቂጣ አልበላችሁም፥ የወይን ጠጅ ወይም ሌላ የሚያሰክር መጠጥ አልጠጣችሁም፤ ይህን ያደረግሁት እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደሆንህ ታውቁ ዘንድ ነው። 7 ወደዚህ ስፍራ በደረሳችሁ ጊዜ የሐሴንቦን ንጉሥ ሴዎንና የባሳን ንጉሥ ዐግ ሊወጉን መጡ፤ ሆኖም ድል አደረግናቸው። 8 ምድራቸውንም ወስደን ለሮቤላውያን ለጋዳውያንና ለምናሴ ነገድ እኩሌታ ርስት አድርገን ሰጠን። 9 እንግዲህ የምታደርጉት ሁሉ እንዲከናወንላችሁ፤ የዚህ ኪዳን ቃሎች በጥንቃቄ ተከተሉ። 10 እናንተ ሁላችሁ መሪዎቻችሁና አለቆቻችሁ፥ ሽማግሌዎቻችሁና ሹሞቻችሁ እንዲሁም ሌሎች የእስራኤል ሰዎች ሁሉ ዛሬ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት ቆማችኋል፤ 11 ልጆቻችሁና ሚስቶቻችሁ እንጨታችሁን እየፈለጡ ውሃዎቻችሁንም እየቀዱ በሰፈራችሁ የሚኖሩ መጻተኞችም አብረአችሁ ቆመዋል። 12 እዚህ የቆማችሁ፥ እግዚአብሔር ዛሬ ከእናንተ ጋር ወደ ሚያደርገውና በመሐላ ወደሚያጸናው ኪዳን፥ከእግዚአብሔር ከአምላካችሁ ጋር ትገቡ ዘንድ ለእናንተ በሰጣችሁ ተስፋና፥ 13 ለአባቶቻችሁ ለአብርሃም፥ ለይስሐቅና ለያዕቆብ በማለላቸው መሠረት እርሱ አምላካችሁ ይሆን ዘንድ እናንተም ሕዝቡ መሆናችሁን በዛሬው ዕለት ለማረጋገጥ ነው። 14 እኔም ይህ የቃል ኪዳን የማደርገው ከእናንተ ጋር ብቻ አይደለም፤ 15 አብራችሁን በእግዚአብሔር በአምላካችን ፊት እዚህ ከቆማችሁት ጋር ብቻ ሳይሆን ዛሬ እዚህ ከሌሉትም ጋር ነው። 16 በግብፅ ምድር እንዴት እንደኖርንና ወደዚህ ስንመጣም በየአገሮቹ ውስጥ እንዴት እንዳለፍን ራሳችሁ ታውቃላችሁ። 17 በመካከላቸውም አስጸያፊ ነገሮቻቸውን፦ የእንጨትና የድንጋይ፥ የብርና የወርቅ ጣዖቶቻቸውን አይታችኋል፤ 18 የእነዚህን ሕዝቦች አማልክት ለማምለክ ልቡን ከእግዚአብሔር ከአምላካችን የሚመልስ ወንድ፥ ሴት፥ቤተ ሰብ፥ ወይም ጎሣና ነገድ ዛሬ ከመካከላችሁ አይገኙ፤ ከመካከላችሁ እንዲህ ያለውን መራራ መርዝ የሚያወጣ ሥር እንዳይኖር ተጠንቀቁ። 19 እንዲህ ያለው ሰው የዚህን ቃል ኪዳን በሚሰማበት ጊዜ በልቡ ራሱን በመባረክ፦ እንደ ልቤ ግትርነት ብመላለስም እንኳ ሰላም አለኝ ብሎ ያስባል። ይህም እርጥቡን ከደረቁ ጋር ያጠፋል። 20 እግዚአብሔር ለዚህ ሰው ፈጽሞ ምሕረት አያደርግለትም፥ ቁጣውና ቅናቱ በእርሱ ላይ ይነድበታል፤ በዚህ መጽሐፍ የተጸፉት ርግማን ሁሉ ይወርድበታል፤ እግዚአብሔርም ስሙን ከሰማይ በታች ይደመስሰዋል። 21 በዚህ የሕግ መጽሐፍ በተጻፈው የኪዳኑ ርግማን መሠረት እግዚአብሔር እርሱን ከእስራኤል ነገዶች ሁሉ ለጥፋት ይለየዋል። 22 የሚቀጥለው ትውልድ ከእናንተ በኋላ የሚተኩት ልጆቻችሁና ከሩቅ አገር የሚመጡ እንግዶች በምድሩቱ የደረሰውን ታላቅ መቅሠፍትና እግዚአብሔር ያመጣባቸውን በሽታዎች ያያሉ፤ 23 ምድሩቱ በሙሉ የተቃጠለ ጨውና ዲን ዐመድ ትሆናለች፤ አንዳች ነገር አይተከልባት፤ ምንም ነገር አያቆጠቁጥባትም። የሚያድግ ተክል አይገኝባትም። የምደርስባት ውድመት እግዝክአብሔር በታላቅ ቁጣ እንደ ገለባበጣቸው እንደሰዶምና ገሞራ እንደ አዳማና ሊባዮ ጥፋት ይሆናል። 24 አሕዛብም ሁሉ፤ እግዚአብሔር በዚች ምድር ላይ ይህን ለምን አደረገባት? ይህ አስፈሪና የሚነድ ቁጣስ ለምን መጣባት? ብለው ይጠይቃሉ። 25 ሕዝቡም እንዲህ ይላሉ፦ የአባቶቻቸው አምላክ እግዚአብሔር ከግብፅ ምድር ያወጣቸውንና ከእነርሱም ጋር ያደረጉትን ቃል ኪዳን ሕዝቡ ስለ ተዉ ነው፤ 26 ወጥተውም የማያውቋቸውን እርሱም ያላዘዛቸውን ሌሎችን አማልክት ስለአመለኩአቸውና ስለሰገዱላቸውም ነው። 27 ስለዚህ በዚህ መጽሐፍ የተጸፈውን ርግማን ሁሉ እስኪያመጣባት ድረስ የእግዚአብሔር ቁጣው በዚህች ምድር ላይ ነደደ። 28 እግዚአብሔር በታላቅ አስፈሪነት፥በቁጣና በንዴት ከምድራቸው ነቀላቸው፤ ወደ ሌላም ምድር ጣላቸው የሚል ይሆናል። 29 ምስጢር የሆነው ለአምላካችን ለእግዚአብሔር ነው፤ የተገለጠው ግን የዚህን ሕግ ቃል ሁሉ ለዘላለም እንድንተገብረው ዘንድ የኛና የልጆቻችን ነው።



Deuteronomy 29:1

እነዚህ ሙሴ እንዲናገር እግዚአብሔር ያዘዘው ቃሎች ናቸው

ይህ ሙሴ የሚናገረውን ቃል ያመለክታል።

በሞዓብ ምድር

ይህ እስራኤላውያን ወደ ከነዓን ምድር ከመግባታቸው በፊት ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ የቆዩበት ስፍራ ነው። “በሞዓብ ምድር እያሉ”

በኮሬብ -- በኪዳኑ ውስጥ ተጨምረው የነበሩት ቃላት

እነዚህ ተጨማሪ ትዕዛዛት በአዲሱ ምድራቸው በሚቀመጡበት ጊዜ ሕዝቡ የእግዚአብሔርን ኪዳን በተሻለ ሁኔታ ተግባራዊ እንዲያደርጉት የተሰጣቸው ነበር። እነዚህ አዲስ ትዕዛዛት የሌላ ቃል ኪዳን ሳይሆኑ በመጀመሪያው ኪዳን ላይ ተጨማሪዎች ነበሩ።

Deuteronomy 29:2

እግዚአብሔር በዐይኖቻችሁ ፊት ያደረገውን ሁሉ አይታችኋል

እግዚአብሔር ያደረገውንና እነርሱም ያዩትን እንዲያስታውሱ እግዚአብሔር ይጠብቅባቸዋል። እዚህ ጋ “ዐይኖች” ሙሉውን ሰው የሚወክሉ ሲሆኑ ሰውየው ባየው ነገር ላይ አጽንዖት ይሰጣል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ያደረገውን እንድታዩና እንድታስታውሱ እርሱ ያደረገውን ሁሉ አይታችኋል። (See: Synecdoche)

ዐይኖቻችሁ ያዩአቸው ታላላቅ መከራዎች

እዚህ ጋ “ዐይኖች” ያዩትን እንዲያስታውሱ እግዚአብሔር እንደሚጠብቅባቸው አጽንዖት ይሰጣል። አ.ት፡ “ሕዝቡ በከፍተኛ ሁኔታ መሰቃየቱን እራሳችሁ አይታችኋል” (See: Synecdoche)

ዐይኖቻችሁ

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “የአንተ” የሚለው ቃል እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

ምልክቶቹንና እነዚያን ታላላቅ ድንቆች

“ምልክቶች” እና “ድንቆች” የሚሉት ቃላት ሁለቱም የሚያመለክቱት እግዚአብሔር በግብፅ ላይ የላካቸውን መቅሰፍቶች ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ያደረጋቸውን ኃይለኛ ነገሮች ሁሉ” (See: Doublet)

እግዚአብሔር የሚያውቅ ልቦና፣ የሚያይ ዐይን ወይም የሚሰማ ጆሮ አልሰጣችሁም ነበር

ሕዝቡ ልብ፣ ዐይንና ጆሮ አላቸው። ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር ካዩትና ከሰሙት እግዚአብሔር ማን እንደሆነ፣ እንዴት እና ለምን እርሱን መታዘዝ እንደሚኖርባቸው እንዲያስተውሉ አላደረጋቸውም ይላል። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እንድታውቁ ልብን ሰጥቷችኋል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ማስተዋል እንድትችሉ አድርጓችኋል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 29:7

የሐሴቦን ንጉሥ ሴዎን እና የባሳን ንጉሥ ዐግ

እነዚህን ስሞች በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

በእኛ ላይ መጡብን

እዚህ ጋ “በእኛ ላይ” የሚያመለክተው ሙሴንና የእስራኤልን ሕዝብ ነው። (See: Inclusive “We”)

የዚህን ቃል ኪዳን ቃላት ጠብቁ፣ አድርጓቸውም

እነዚህ ሁለት ሐረጎች የሚሉት ተመሳሳይ ነገር ሲሆን ሕዝቡ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት መታዘዝ እንዳለባቸው አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “የዚህን ቃል ኪዳን ቃሎች ሁሉ ታዘዙ” (See: Parallelism)

Deuteronomy 29:10

በሰፈርህ ውስጥ በመካከልህ -- እንጨትህን -- ውሃህን

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ’ እና “የአንተ” የሚሉት ቃላት እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥር ናቸው። (See: Forms of You)

በሰፍርህ ያሉ መጻተኞች፣ ከእርሱም እንጨት የሚቆርጡልህና ውሃ የሚቀዱልህ

በእስራኤላውያን መካከል ብዙ መጻተኞች ነበሩ። አ.ት፡ “በሰፈርህ ውስጥ በመካከልህ የሚኖሩ መጻተኞች፣ ከእነርሱ እንጨት የሚቆርጡልህ ውሃ የሚቀዱልህ” (See: Generic Noun Phrases)

Deuteronomy 29:12

አምላክህ እግዚአብሔር ዛሬ ከአንተ ጋር በመሓላ ወደሚያደርገው ወደ አምላክህ ወደ እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ለመግባት

“በቃል ኪዳኑ ልትስማማ እና አምላክህ እግዚአብሔር የሚያዝህን ሁሉ ለመታዘዝ እንድትምል”

ለራሱ ሕዝብ

“ለእርሱ ብቻ የሚሆን የሕዝብ ወገን”

Deuteronomy 29:14

እኔ የማደርገውን

x

Deuteronomy 29:17

ዛሬ ከአምላካችን ከእግዚአብሔር ልቡ የሚመለስ

እዚህ ጋ “ልብ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ሲሆን “መመለስ” ማለት መታዘዝን ማቆም ነው። አ.ት፡ “ከእንግዲህ አምላካችንን እግዚአብሔርን የማይታዘዝ” (See: Synecdoche)

የትኛውም መራራ መርዝ የሚያበቅል ሥር

ሙሴ በድብቅ ሌላ አምላክ ስለሚያመልክ ሰው ሲናገር እርሱን እንደ ሥር እና ያንን አምላክ ለማገልገል የሚሠራውን ክፉ ሥራና ሌሎችም እንዲያደርጉት የሚያበረታታውን ሰዎችን እንደሚመርዝ መራራ እጽዋት ቆጥሮ ይናገራል።(ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ያ ሰው

በቁጥር 18 የተገለጸው ሰው ነው።

በልቡ ራሱን የሚባርክ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ራሱን እንኳን ደስ ያለህ የሚል” ወይም “ራሱን የሚያበረታታ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በልቤ ግትርነት ብመላለስም

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን ለመታዘዝ እምቢ እያልኩኝም እንኳን” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ይህ እርጥቡን ከደረቁ ጋር የሚያጠፋ ይሆናል

እዚህ ጋ “እርጥብ” እና “ደረቅ” የሚሉት ቃላት ጻድቅና ክፉ የሆኑትን ሰዎች የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገሮች ናቸው። ይህ “እያንዳንዱን” የሚል ጥምረት ይፈጥራል። አ.ት፡ “ይህ እግዚአብሔር በምድሪቱ የሚኖሩትን ጻድቅና ክፉ የሆኑትን ሁለቱንም ዓይነት ሰዎች እንዲያጠፋቸው ያደርገዋል” (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር እና Merism የሚለውን ተመልከት))

እርጥብ -- ደረቅ

እነዚህ ስማዊ ቅጽሎች እንደ ስም ሊተረጎሙ ይችላሉ። አብዛኛውን ጊዜ ምድሪቱ ደረቅ ስለምትሆንና ሰዎች ሰብላቸው እንዲበቅል ዝናብ ስለሚፈልጉ እነዚህ ቃላት “ሕያው - ምውት” ወይም “ጥሩ -- መጥፎ” ለሚሉት ዘይቤአዊ አነጋገሮች ናቸው። አ.ት፡ “እርጥብ ነገሮች -- ደረቅ ነገሮች” ወይም “ጥሩ ሰዎች -- መጥፎ ሰዎች” (ስማዊ ቅጽል እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 29:20

የእግዚአብሔር ቁጣና ቅንዓት ይነዳል

ልክ እሳት በኃይል እንደሚነድ የእግዚአብሔር ቁጣና ቅንዓትም በኃይል ሊነድ ይችላል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር የቅንዓቱ ቁጣ እንደ እሳት ይግላል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የእግዚአብሔር ቁጣና ቅንዓቱ

እዚህ ጋ “ቅንዓት” የሚለው ቃል “የእግዚአብሔርን ቁጣ” ያብራራል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር የቅንዓቱ ቁጣ” (See: Hen- diadys)

የተጻፉትን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እኔ የጻፍኩትን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በዚህ መጽሐፍ የተጻፉት እርግማኖች ይመጡበታል

ሙሴ እርግማኖቹን በድንገት በሚያጠቃቸው ሰው መስሎ ይገልጻቸዋል። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 28፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ዘይቤአዊ አነጋገር እና ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር ስሙን ከሰማይ በታች ይደመስሰዋል

ይህ ማለት እግዚአብሔር ሰውየውንና ቤተሰቡን ፈጽሞ ያጠፋቸዋል። ወደፊት ሰዎች አያስታውሱትም። በዘዳግም 7፡24 ላይ ተመሳሳይ ሐረግ ይታያል።

Deuteronomy 29:22

የሚመጣው ትውልድ፣ ከእናንተ በኋላ የሚነሡት ልጆቻችሁ

“ከእናንተ በኋላ -- ልጆቻችሁ” የሚሉት ቃላት “የሚመጣው ትውልድ” ማን መሆኑን ይናገራሉ።

በዚህች ምድር ላይ የሆኑት መቅሰፍቶችና እግዚአብሔር እንዲታመሙበት ያደረጋቸው በሽታዎች

“እግዚአብሔር የከነዓንን ምድር በመቅሰፍትና በበሽታ እንዴት እንደረገማት”

ምድሩ ሁሉ ዲንና የሚቃጠል ጨው ሆነው በሚያዩበት ጊዜ

ሰዎች መሬቱ ምንም ነገር እንዳያበቅል ዲንና ጨው ያደርጉበታል። “እግዚአብሔር ምድሪቱን በዲንና በጨው እንዳቃጠላት በሚያዩበት ጊዜ”

ምንም ነገር የማይዘራበት ወይም ፍሬ የማያፈራበት ስፍራ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማንም ዘር ሊዘራበት የማይችልበትና ሰብሉ ፍሬ የማያፈራበት ስፍራ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሰዶምና ገሞራ እንደ ተገለበጡ

“ተገለበጡ” የሚለው የነገር ስም እንደ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሰዶምንና ገሞራን ፈጽሞ እንዳጠፋቸው ጊዜ”

አዳማ እና ሲባዮ

እነዚህ እግዚአብሔር ከሰዶምና ገሞራ ጋር ያጠፋቸው ከተሞች ስሞቻቸው ናቸው።(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በንዴቱና በመዓቱ

የነገር ስም የሆኑት “ንዴት” እና “ቁጣ” በመሠረቱ ትርጉማቸው አንድ ነው፣ በመሆኑም እንደ ቅጽላዊ ሐረግ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በጣም በተቆጣ ጊዜ” (See: Doublet)

ከሌሎች ሀገሮች ሁሉ ጋር በመሆን --ምንድነው? በማለት ይናገራሉ

ይህ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ከሌሎች ሀገራት ሁሉ ጋር በመሆን እግዚአብሕር በምድሪቱ ላይ ይህንን ለምን እንዳደረገና ይህ የቁጣው ግለትስ ትርጉሙ ምንድነው በማለት ይጠይቃሉ” (ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

ከሌሎች ሀገሮች ሁሉ ጋር በመሆን -- ይናገራሉ

“ዘሮቻችሁና የሌሎች ሀገራ ሰዎች ሁሉ -- ይላሉ”

ይህ የታላቅ ቁጣ ግለት ትርጉሙ ምንድነው?

ጸሐፊው በሁለት ቃላት አማካይነት የሚያስተላልፈው አንድ አሳብ ነው። አ.ት፡ “የዚህ አስፈሪ ቁጣ ትርጉሙ ምንድነው?” (See: Hendiadys)

Deuteronomy 29:25

የአባቶቻቸውን አምላክ የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን ስለተዉ ነው

ይህ “እግዚአብሔር በዚህች ምድር ላይ ይህንን ያደረገው ለምንድነው?” ለሚለው መልስ ነው (ዘዳግም 29፡24)። “እስራኤላውያን የቃል ኪዳኑን ተስፋና ሕግ ስላልተከተሉ እግዚአብሔር በምድሪቱ ላይ ይህንን አድርጓል”

ሌሎች አማልክትን አገለገሉ፣ ሰገዱላቸውም

“ሌሎች አማልክትን ታዘዙ፣ አመለኳቸውም”

Deuteronomy 29:27

የእግዚአብሔር ቁጣ በዚህች ምድር ላይ ነዷል

ሙሴ የእግዚአብሔርን መቆጣት ከአንድ እሳት ከሚለኩስ ሰው ጋር ያነጻጽራል። ይህ እግዚአብሔር እርሱን የሚያስቆጣውን የትኛውንም ነገር ስለሚያጠፋበት ኃይሉ አጽንዖት ይሰጣል፤ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር አይችልም። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በዚህች ምድር ላይ በጣም ተቆጥቷል” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በዚህች ምድር ላይ እንዲያመጣባት

እዚህ ጋ “ምድር” ሕዝቡን የሚወክል ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ያመጣባቸው ዘንድ የዚህ ምድር ሰዎች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የተጻፉትን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እኔ የጻፍኩትን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር ከምድራቸው ነቅሏቸዋል -- ጥሎአቸዋል

እስራኤል እግዚአብሔር ከአትክልት ስፍራ ነቅሎ ከጣለው መጥፎ ተክል ጋር ተነጻጽሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ከምድራቸው አስወግዷቸዋል -- እንዲሄዱም አስገድዷቸዋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በንዴት፣ በቁጣና በታላቅ መዓት

በመሠረቱ “ንዴት”፣ “ቁጣ” እና “መዓት” የሚሉት ቃላት ትርጉማቸው ተመሳሳይ ሲሆን በእግዚአብሔር ቁጣ ታላቅነት ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “እጅግ ታላቅ በሆነ ቁጣው” ወይም “እጅግ ስለተቆጣ” (See: Doublet)

Deuteronomy 29:29

ምስጢር የሆኑት ነገሮች የአምላካችን የእግዚአብሔር ብቻ ናቸው

“አምላካችን እግዚአብሔር ያልገለጣቸውና እርሱ ብቻ የሚያውቃቸው አንዳንድ ነገሮች”

የተገለጡት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እርሱ የገለጣቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የዚህን ሕግ ቃሎች በሙሉ እንድናደርጋቸው

x


Chapter 30

1 በፊታችሁ ያስቀመጥሁት ይህ በረከትና መርገም ሁሉ በእናንተ ላይ ሲመጣና አምላካችሁ እግዚአብሔር በትኖአችሁ ከምትኖሩበት አሕዛብ መካከል ሆናችሁ፤ 2 ወደ ልባችሁ ተመልሳችሁ ነገሮቹን በምታስተውሉበት ጊዜ፥ እንዲሁም ዛሬ እኔ በማዝዛችሁ ሁሉ መሠረት እናንተና ልጆቻችሁ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ተመልሳችሁ በፍጹም ልባችሁና በፍጹም ነፍሳችሁ እርሱን ስትታዘዙ፤ 3 እግዚአብሔር አምላካችሁ ምርኮአችሁን ይመልስላችኋል፤ ይራራላችሁማል፤ እናንተን ከበተነበት አሕዛብ መካከል እንደ ገና ይሰበስባችኋል። 4 ከሰማይ በታች እጅግ ሩቅ ወደ ሆነ ምድር ብትጋዙ እንኳ እግዚአብሔር አምላካችሁ ከዚያ ይሰበስባችኋል፤ መልሶም ያመጣችኋል። 5 የአባቶቻችሁ ወደ ሆነችው ምድር ያመጣችኋል፤ እናንተም ትወርሱታላችሁ፤ ከአባቶቻችሁ ይበልጥ ያበለጽጋችኋል፤ያበዛችሁማል። 6 እግዚአብሔር አምላካችሁን በፍጹም ልባችሁና በፍጹም ነፍሳችሁ እንድትወዱት፤በሕይወትም እንድትኖሩ እግዚአብሔር አምላካችሁ የእናንተንና የዘራችሁን ልብ ይገርዛል። 7 አምላካችሁ እግዚአብሔር ይህን ርግማን ሁሉ በሚጠሉአችሁና በሚያሳድዱአችሁ ጠላቶቻችሁ ላይ ያደርገዋል። 8 እናንተም ተመልሳችሁ ለእግዚአብሔር ትታዘዛላችሁ፥ ዛሬ እኔ የማዛችሁን ትእዛዛ ሁሉ ትጠብቃላችሁ። 9 በዚያም እግዚአብሔር በእጃችሁ ሥራ ሁሉን በወገባችሁ ፍሬ በእንስሳታችሁ፥ ግልገሎችና በምድራችሁ ሰብል እጅግ ያበለጽጋችኋል። በአባቶቻችሁ ደስ እንደ ተሰኘ ሁሉ እግዚአብሔር እናንተንም በማበልጸግ ደስ ይለዋልና። 10 ይህም የሚሆነው አምላካችሁን እግዚአብሔርን ከታዘዛችሁና በዚህ የሕግ መሕሐፍ የተጻፉትን ትእዛዙንና ሥርዓቱን በመጠበቅ በፍጹም ልባችሁና በፍጹም ነፍሳችሁ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ስትመለሱ ነው። 11 ዛሬ የምሰጣችሁ ትእዛዝ ይህን ያህል አስቸጋሪ ወይም ከእናንተ የራቀ አይደለም። 12 እንድንፈጽሙት አምጥቶ ይነግረን ዘንድ ማን ወደ ሰማይ ይወጣል? እንዳትሉ በሰማይ አይደለም። 13 ደግሞም እንድናደርገው አምጥቶ ይነግረን ዘንድ ማን ባሕሩን ይሻገራል? እንዳትሉም ከባሕር ማዶ አይደለም። 14 ነገር ግን ቃሉ ለእናንተ በጣም ቅርብ ነው፤ ታደርጉትም ዘንድ በአፋችሁና በልባችሁ ውስጥ ነው። 15 እነሆ ዛሬ ሕይወትንና በረከትን፥ ሞትንና ጥፋትን በፊታችሁ አኑሬአለሁ። 16 እግዚአብሔር አምላካችሁን እንድትወዱ በመንገዱም እንድትሄና ትእዛዙን፥ ሥርዓቱንና ሕጉን እንድትጠብቁ አዝዛችኋል፤ ከዚያም በሕይወት ትኖራላችሁ፥ ትበዛላችሁም፤ አምላካችሁም ትወርሱአት ዘንድ በምትገቡበት ምድር ይባርካችህኋል። 17 ዳሩ ግን ልባችሁን ወደ ኋላ በመለሰና ባትታዘዙ ለሌሎች አማልክት ለመስገድ ብትታለሉና ብታመልኩአችሁ፤ 18 በርግጥ እንደምትጠፉ እኔ በዛሬው ዕለት እነግራችኋለሁ፤ ዮርዳኖስን ተሻግራችሁ ትወርሱአት ዘንድ በምትገቡባት ምድር ብዙ አትኖሩባትም። 19 ሕይወትንና ሞትን፥ በረከትንና ርግማንን በፊታችሁ እንዳስቀመጣችሁ ዛሬ ሰማይንና ምድርን ምስክር አድርጌ እጠራችኋለሁ። እንግዲህ እናንተና ልጆቻችሁ በሕይወት እንድትኖሩ ሕይወትን ምረጡ፤ 20 ይኸውም እግዚአብሔር አምላካችሁን እንድትወዱ ቃሉን እንድታደምጥና ከእርሱ ጋር እንድትጣበቁ ነው። ምክንያቱም እግዚአብሔር ሕይወታችሁ ነው፤ ለአባቶቻችሁ ለአብርሃም፥ ለሕስሐቅና ለያዕቆብ ሊሰጣቸው በማለላቸው ምድር ረጅም ዕድሜ ይሰጣችኋል።



Deuteronomy 30:1

እነዚህ ነገሮች ሁሉ በመጡብህ ጊዜ

እዚህ ጋ “እነዚህ ነገሮች” የሚያመለክቱት በምዕራፍ 28 – 29 የተዘረዘሩትን በረከቶችና እርግማኖች ነው። “በመጡብህ” የሚለው ቃል የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ትርጉሙ ሲደርስብህ ማለት ነው። አ.ት፡ “እነዚህ ነገሮች ሁሉ በሚደርሱብህ ጊዜ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በፊትህ ያስቀመጥኩት

ይህ በፊት ለፊታቸው ያስቀመጠው ዕቃ ይመስል መልኩ ሙሴ ለሕዝቡ ስለ ነገራቸው በረከቶችና እርግማኖች ይናገራል። አ.ት፡ “አሁን ስለነገርኳችሁ ጉዳይ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ትዝ ይበሉህ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አስታውሳቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በሌሎች ሕዝቦች ሁሉ መካከል

“በሌሎች ሕዝቦች ውስጥ በምትኖርበት ጊዜ”

አውጥቶሃል

“እንድትሄድ አስገድዶሃል”

ድምፁን ታዘዘው

እዚህ ጋ “ድምፅ” የሚያመለክተው እግዚአብሔር የሚናገረውን ነው። አ.ት፡ “እርሱ የሚለውን ታዘዝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በሙሉ ልብህና በሙሉ ነፍስህ

እዚህ ጋ “ልብ” እና “ነፍስ” የአንድን ሰው ውስጣዊ ማንነት የሚያመለክቱ ፈሊጣዊ አነጋገሮች ናቸው። እነዚህ ሁለቱ ሐረጎች በአንድ ላይ “ፍጹም” ወይም “በቅንነት” ለማለት ጥቅም ላይ ውለዋል። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

ምርኮኛነትህን ይቀይረዋል

“ከምርኮኝነት ነጻ ያወጣሃል”። የነገር ስም የሆነው “ምርኮኝነት” እንደ ግሳዊ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ከማረኩህ ከእነርሱ ነጻ ያወጣሃል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 30:4

ከተማረኩት ሰዎችህ ማናቸውም እጅግ ሩቅ ስፍራ ላይ ቢሆኑ

“እነዚያ የተማረኩት ሰዎችህ እጅግ ሩቅ በሆነ ስፍራ የሚኖሩ ቢሆኑም እንኳን”

ከሰማያት በታች

“ከጠፈር በታች” ወይም “በምድር ላይ”

Deuteronomy 30:6

ልብህን ይገርዛል

ይህ በቀጥታ ሥጋን ማስወገድ አይደለም። ይህ ማለት እግዚአብሔር ኃጢአታቸውን ያስወግዳል፣ እርሱን እንዲወዱትና እንዲታዘዙትም ያስችላቸዋል ማለት ነው። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በሙሉ ልብህና በሙሉ ነፍስህ

እዚህ ጋ “ልብ” እና “ነፍስ” የአንድን ሰው ውስጣዊ ማንነት የሚያመለክቱ ፈሊጣዊ አነጋገሮች ናቸው። እነዚህ ሁለቱ ሐረጎች በአንድ ላይ “ፍጹም” ወይም “በቅንነት” ለማለት ጥቅም ላይ ውለዋል። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Doublet የሚለውን ተመልከት)

የእግዚአብሔርን ድምፅ ታዘዝ

እዚህ ጋ “ድምፅ” ማለት እግዚአብሔር የሚናገረውን ማለት ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የሚናገረውን ታዘዝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እነዚህን እርግማኖች ሁሉ በጠላቶችህ ላይ ያደርጋል

ሙሴ እርግማኖቹን አንድ ሰው በሌላው አናት ላይ ሊያደርግ እንደሚችለው ሸክም ወይም መሸፈኛ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “ጠላቶችህ በእነዚህ እርግማኖች ምክንያት እንዲሰቃዩ ያደርጋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 30:9

የእጅህን ሥራ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “በምትሠራው ሥራ ሁሉ” (See: Synecdoche)

በሰውነትህ ፍሬ -- በከብቶችህ ፍሬ -- በመሬትህ ፍሬ

እነዚህ ሦስት ሐረጎች “በልጆች -- በጥጆች -- በሰብሎች” ለሚለው የአነጋገር ዘይቤ ናቸው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 28፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

Deuteronomy 30:11

ትደርስበት ዘንድ ለአንተ እጅግ ሩቅ አይደለም

አንድ ሰው ቁሳዊ አካል ላይ ሊደርስ እንደሚችል ሁሉ ትዕዛዛቱ አንድ ሰው እንዲያደርግ የሚፈልገውን ከትዕዛዛቱ መረዳት እንደሚቻል ሙሴ ይናገራል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እንድታደርግ የሚፈልግብህን ለመረዳት በጣም አስቸጋሪ አይሆንብህም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እናደርገው ዘንድ እንድንሰማው ማን ወደ ሰማይ ወጥቶ ያወርድልናል?

እዚህ ጋ ሙሴ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄን በመጠቀም የእስራኤል ሕዝብ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ለማወቅ በጣም አስቸጋሪ እንደሚሆንባቸው ማሰባቸው ላይ አጽንዖት ይሰጣል። ይህ ጥያቄ እንደ ንግግር ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ለመማር ወደ ሰማይ መጓዝ አለበት፣ ከዚያም ልንታዘዛቸው እንችል ዘንድ ምን እንደ ሆኑ ሊነግረን መመለስ አለበት” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 30:13

እናደርገው ዘንድ ልንሰማው ማን ባህሩን ተሻግሮ ያምጣልን?

ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የእስራኤል ሕዝብ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ማወቅ በጣም አስቸጋሪ ነው ብለው የሚያስቡበትን አሳብ ይቀጥላል። ይህ ጥያቄ እንደ ንግግር ሆኖ ሊተርጎም ይችላል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ለመማር አንድ ሰው ባህሩን አቋርጦ መጓዝ ከዚያም ተመልሶ ምን እንደሆኑ ሊነግረን ያስፈልጋል” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

በአፍህና በልብህ

ይህ ማለት ሕዝቡ ቀደሞውኑ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ያውቃሉ፣ ለሌሎችም ሊነግሯቸው ይችላሉ። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 30:15

በፊትህ አስቀምጫለሁ

አንድን ነገር ሌላው ሰው ሊያይ በሚችልበት ማስቀመጥ ስለ አንድ ነገር ለአንድ ሰው የመንገር ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ስለ ጉዳዩ ነግሬሃለሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሕይወትንና መልካምን፣ ሞትንና ክፉን

ግልጽ ያልሆነውን መረጃ ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “መልካም የሆነውንና በሕይወት እንድትኖር የሚያደርግህን፣ ክፉ የሆነውንና እንድትሞት የሚያደርግህን” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

መብዛት

በቁጥር እጅግ መጨመር

Deuteronomy 30:17

ልብህ ቢመለስ -- ይልቱንም ቢማረክና ለሌሎች አማልክት ቢሰግድና ቢያመልካቸው

እዚህ ጋ “ልብ” የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ለእግዚአብሔር ያለህን ታማኝነት ብታቆም -- እና በምድሪቱ የሚኖሩ ሰዎች እንድትሰግድና ሌሎች አማልክትን እንድታመልክ ቢያባብሉህ” (Synecdoche እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ዛሬ ለአንተ -- ቀኖችህ እንደማይረዝሙ

x

Deuteronomy 30:19

ሰማይና ምድርን ምስክር እንዲሆኑ እጠራለሁ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ሙሴ ለሚናገረው ምስክሮች እንዲሆኑ በሰማይና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ይጠራል ወይም 2) ሙሴ እንደ ሰዎች ቆጥሯቸው ለሰማይና ለምድር ይናገራል፣ እርሱ ለሚናገረው ምስክሮች እንዲሆኑም ይጠራቸዋል። (See: (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት and Personification and Apostrophe)

በአንተ ላይ ምስክር እንዲሆኑ

“ክፉ ነገሮችን ስለማድረግህ ለመናገር ፈቃደኛ እንዲሆን”

ዛሬ በአንተ ላይ

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ ቡድን አድርጎ ይናገራል። (See: Forms of You)

ድምፁን ታዘዝ

እዚህ ጋ “ድምፅ” እግዚአብሔር የሚናገረውን ያመለክታል። አ.ት፡ “እርሱ የሚለውን ታዘዝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእርሱ ጋር እንድትጣበቅ

“በእርሱ ላይ እንድትተማመን”

እርሱ ሕይወትህና የቀኖችህ ርዝመት ነውና

እነዚህ ሐረጎች ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸውና እግዚአብሔርን የሚገልጹ ፈሊጣዊ አነጋገሮች ሲሆኑ ሕይወትን የሚሰጥና የሰዎችን የሕይወት ዘመን የሚወስን እርሱ መሆኑን አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “ረጅም ሕይወት እንድትኖር የሚያስችልህ እግዚአብሔር ብቻ ነው” (Doublet እና ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለአባቶቻችሁ የማለውን

ሞላላው ሊሞላ ይችላል። አ.ት፡ “ለአባቶቻችሁ ሊሰጣችሁ ምሏል” (See: Ellipsis)


Chapter 31

1 ሙሴም ወጥቶ እነዚህን ቃሎች ለእስራኤል በሙሉ ነገራቸው። 2 እንዲህም አላቸው፦ መቶ ሃያ ዓመት ሆኖኛል ከእንግዲህ መወጣትና መግባት አልችልም፤ እግዚአብሔርም ዮርዳኖስን አትሻገርም ብሎኛል፥ 3 እግዚአብሔር አምላካችሁ ራሱ በፊታችሁ ቀድሞ ይሄዳል፤ እነዚህንም አሕዛብ ከፊታችሁ ያጠፋቸዋል፤ እናንተም ምድራቸውን ትወርሳላችሁ፤ እግዚአብሔር እንደ ተናገረው፤ ኢያሱም እናንተን ቀድሞ ይሻገራል። 4 እግዚአብሔር የአሞራውያንን ነገሥታት ሴዎንንና ዐግን ከነምድራቸው እንዳጠፋቸው እነዚህንም ያጠፋቸዋል። 5 እግዚአብሔር እነርሱን በፊታችሁ አሳልፎ ይሰጣችኋል፤ እናንተም ያዘዝኋችሁን ሁሉ በእነርሱ ላይ ታደርጋላችሁ። 6 ብርቱና ደፋር ሁኑ፥ አትፍሯቸው ወይም አትደንግጡል አላቸው። እግዚአብሔር አምላካችሁ ከእናንት ጋር ይሄዳልና አይተዋችሁም አይጥላችሁምም። 7 ከዚያም ሙሴ ኢያሱን ጠርቶ በእስራኤል ሁሉ ፊት እንዲህ አለው፦ እግዚአብሔር ለአባቶቻቸው ሊሰጥ ወደ ማለላቸው ምድር ከዚህ ሕዝብ ጋር አብረህ ስለምትገባ፤ ምድሪቱን ርስታችው አድርገህ ስለምታከፋፍል በርታ፤ ደፋርም ሁን። 8 እግዚአብሔር ራሱ በፊትህ ይሄዳል፤ ከአንተም ጋር ይሆናል፤ ፈጽሞ አይለይህም፤ አተውህምም አትፍራ ተስፋም አትቁረጥ። 9 ሙሴም ይህን ሕግ ጽፎ የእግዚአብሔርን የኪዳን ታቦት ለሚሸከሙ፥ ለሌዊ ልጆች፤ ለካህቱና ለእስራኤል አለቆች ሁሉ ሰጠ። 10 ከዚያም በኋላ ሙሴ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፤ዕዳ በሚተውበት የዳስ በዓልም በሚከበርበት በየሰባቱ ዓመት መጨረሻ 11 እስራኤል ሁሉ እርሱ በሚመርጠው ስፍራ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ፊት ሲታይ ይህ ሕግ በእነርሱ ፊት በጆሮአቸው ታነባቸዋላችሁ። 12 እነርሱም ይስሙና አምላካችሁን እግዚአብሔርን መፍራት ይማሩ ዘንድ የዚህን ሕግ ቃል ሁሉ በጥንቃቄ እንዲከተሉ ሕዝቡን ይኸውም ወንዶችን፥ ሴቶችንና ልጆቻቸሁንና በከተሞቻችሁን የሚኖረውንም መጻተኛ ሰብስቡ። 13 ዮርዳኖስን ተሻግራችሁ በምትወርሷት ምድር በምትኖሩበት ዘመን ሁሉ ይህን ሕግ የማያውቁት ልጆቻቸሁም መስማትና አምላካችሁን እግዚአብሔርን መፍራት ሊማሩ ይገባቸዋል። 14 እግዚአብሔር ሙሴን እነሆ የምትሞትበት ቀን ቀርቦአል፥ ትእዛዝ እንድሰጠው ኢያሱን ጥራውና ወደ መገናኛው ድንኳንም ቅረቡ። 15 እግዚአብሔር በድንኳኑ ላይ በደመና ዐምድ ተገለጠ፤ የደመናውም ዐምድ ከድንኳኑ ደጃፍ ላይ ቆመ። 16 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ አለው፦ እነሆ ከአባቶቻችሁ ጋር ልታርፍ ነው፤ ይህም ሕዝብ በሚገባበት ምድር በሚገኙ አማልክት ወዲያውኑ ያመነዝራል፤ እኔን ይተወኛል፤ ከእነርሱም ጋር የገባሁትን ኪዳን ያፈርሳሉ። 17 በዚያም ቀን ቁጣዬ በእነርሱ ላይ ይነዳል፤ እተዋቸዋለሁም። ፊቴንም ከእነርሱ እሰውራለሁ፤ እነርሱም ይጠፋሉ። ብዙ ጥፋትና የከፋ ችግር ይደርስባቸዋል፤ በዚያም ቀን ይህ ጥፋት የደረሰሰብን አምላካችን ከእኛ ጋር ባለመሆኑ አይደለምን? ይላሉ። 18 ወደ ባዕዳን አማልክት በመዞር በፈጸሙት ክፋታቸው የተነሣ በዚያን ቀን ፊቴን ከእነርሱ ፈጽሞ እሰውራለሁ። 19 እንግዲህ ይህን መዝሙር ለራሳችሁ ጻፉና ለእስራኤል ልጆች አስተምሩ። ስለ እኔ ምስክር ይሆንባቸው ዘንድ እንዲዘምሩ አድርጉ። 20 ወተትና ማር ወደምታፈሰውና ለአባቶቻቸው በመሐላ ቃል ወደ ገባህላቸው ምድር ባመጣሃቸው ጊዜ ከበሉና ከጠገቡ፥ ከበለጸጉም በኋላ እኔን ንቀው ኪዳኔንም አፍርሰው ወደ ባዕዳን አማልክት ይዞራሉ፤ እነርሱንም ያመልካሉ። 21 ብዙ ጥፋትና የከፋ ችግር በደረሰባቸው ጊዜ ይህ መዛሙር ምስክር ይሆንባቸዋል። በዘራቸውም አፍ የሚረሳ አይሆንም፤ ወደ ማልሁላቸው ምድር ሳላስገባቸው በፊት ምን ለማድረግ እንደሚያስቡ እንኳን አስቀድሜ አውቃለሁ። 22 ስለዚህም ሙሴ ይህን መዝሙር በዚያን ቀን ጻፈና እስራኤላውያንን አስተማራቸው። 23 እግዚአብሔርም ለነዌ ልጅ ለኢያሱ በር ደፋር ሁን፤ የእስራኤልን ልጆች በመሐላ ቃል ወደ ገባሁላቸው ምድር ታስገባቸዋለህና እኔም ከአንተ ጋር እሆናለሁ በማለት ትእዛዝ ሰጠው። 24 ሙሴ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ የዚህን ሕግ ቃል በመጽሐፍ ጽፎ እንዳበቃ፤ 25 የእስራኤልን የኪዳን ታቦት የሚሸከሙ ሌዋውያንን እንዲህ ሲል አዘዛቸው፤ 26 ይህን የሕግ መጽሐፍ ውሰዱ፤ በዚያም በእናንተ ላይ ምስክር እንዲሆን በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ቃል ኪዳን ታቦት አጠገብ አኑሩት። 27 ዐመፀኞችና አንገተ ደንዳኖች እንደ ሆናችሁ አውቃለሁ፥ተመልከቱ እኔ ዛሬ በሕይወት ከእናንተ ጋር እያለሁ እንኳን በእግዚአሔር ላይ እንደህ ካመፃችሁ ከሞትሁ በኋላማ እንዴት አታደርጉም? 28 ሰማይንና ምድርን ምስክር አድርጌ ጠርቼባቸው ይህን ቃል ይሰሙ ዘንድ ብጆሮኣቸው እንድናገር ፤ የነገድ አለቆቻችሁን በሙሉና ሹሞቻችሁን ሁሉ በፊቴ ሰብስቡ። 29 እኔ ከሞትሁ በኋላ ፈጽማችሁ እንደምትረክሱ ካዘዝኋችሁም መንገድ ዘወር እንደምትሉ አውቃለሁና። በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ድርጊት ስለምትፈጽሙ፤ ይህ የሚሆነው እጆቻችሁ በሠሯቸውም ነገሮች እርሱን ለቁጣ ስለምታነሣሡት በሚመጡት ዘመናት ጥፋት ይደርስባችኋል። 30 ሙሴ የዚህን መዝሙር ቃል ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ድረስ ለተሰበሰበው ለእስራኤል ሕዝብ ሁሉ በጆሮአቸው አሰማ።



Deuteronomy 31:1

የአንድ መቶ ሃያ ዓመት ዕድሜ

“120 ዓመት ዕድሜ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ከእንግዲህ መውጣትና መግባት አልችልም

እዚህ ጋ “መውጣት” እና “መግባት” የተሰኙ ሁለት ጽንፎች በአንድ ላይ አንድ ጤነኛ ሰው ሊያደርግ የሚችለውን ሙሴ ከእንግዲህ ማድረግ አይችልም ማለት ነው። (See: Merism)

አምላክህ -- በፊትህ -- በፊትህ -- ታስወጣቸዋለህ -- በፊትህ

ሙሴ እስራኤላውያኑን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት ቃላት እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

ታስወጣቸዋለህ

“ምድራቸውን ትወስዳለህ”

እግዚአብሔር እንደተናገረው ኢያሱ በፊታችሁ ይሄዳል

“እግዚአብሔር ቃል እንደገባው ኢያሱ መርቶ ወንዙን ያሻግራችኋል”

Deuteronomy 31:4

በአሞራውያን ነገሥታት በሴዎንና በዐግ -- አደረገ

እዚህ ጋ “ሴዎን” እና “ዐግ” ሁለቱን የአሞራውያንን ነገሥታትና ሰራዊታቸውን ያመለክታል። እነዚህን ስሞች በዘዳግም 1፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “በአሞራውያን ነገሥታት በሴዎን፣ በዐግና በሰራዊቶቻቸው ላይ -- አደረገ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 31:7

በእስራኤል ሁሉ ፊት

ይህ ማለት የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ በዚያ ነበሩ ማለት ነው። አ.ት፡ “በእስራኤላውያን ሁሉ ፊት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ብርቱ ሁን፣ ድፍረትም ይኑርህ

“ብርቱና ደፋር ሁን”። ይህንን በዘዳግም 31፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

እንዲወርሱት ታደርጋቸዋለህ

“ምድሪቱን እንዲወስዱ ትረዳቸዋለህ”

Deuteronomy 31:9

ለሌዊ ልጆች ለካህናቱ ሰጣቸው

“ካህናት ለሆኑት ለሌዋውያኑ ሰጣቸው”

ሰባት ዓመት

“7 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ዕዳን ለመተው የተወሰነበት

“ዕዳን ለመሰረዝ”

የመጠለያ በዓል

የዚህ በዓል ሌሎች ስሞች፣ “የመገናኛው ድንኳን በዓል”፣ “የዳስ በዓል”፣ እና “የመሰብሰብ በዓል”። በመከር ጊዜ ገበሬዎች በመስኩ ላይ ጊዜያዊ መጠለያ ይሠሩ ነበር። ይህ በዓል የሚደረገው የዓመቱ መከር ከተሰበሰበ በኋላ ነበር። ይህንን በዘዳግም 16፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

አምላክህ እግዚአብሔር -- ታነበዋለህ

ሙሴ እስራኤላውያኑን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚለው ቃል እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

በመስሚያቸው

“መስማት ይችሉ ዘንድ”

Deuteronomy 31:14

ተመልከት

“እኔ ለምነግርህ ትኩረት ስጥ”

የደመና ዓምድ

ይህ በላይኛው ክፍል ቅርጽ የያዘ ጥቅጥቅ ያለ የጢስ ደመና ነበር

Deuteronomy 31:16

ተመልከት

“እኔ ለምነግርህ ትኩረት ስጥ”

ከአባቶችህ ጋር ታንቀላፋለህ

ይህ “ትሞታለህ” የማለት የትህትና አገላለጽ ነው። አ.ት፡ “ትሞትና ከአንተ በፊት ከሞቱት ቅድመ ቅድም አያቶችህ ጋር አብረህ ትሆናለህ” (See: Euphemism)

ተነሥተው የአመንዝራን ተግባር ይፈጽማሉ

አመንዝራ መሆን ከእግዚአብሔር ሌላ ሌሎች አማልክትን ለማምለካቸው ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ለእኔ አለመታመን ይጀምራሉ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 31:17

ቁጣዬ በእነርሱ ላይ ይነድዳል

እግዚአብሔር ቁጣውን እሳት ከሚለኩስ ሰው ጋር ያነጻጽራል። ይህ እርሱን የሚያስቆጣውን የትኛውንም ነገር በሚያጠፋ በእግዚአብሔር ኃይል ላይ አጽንዖት ይሰጣል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ቁጣዬን በእነርሱ ላይ አነድዳለሁ” ወይም “በእነርሱ ላይ እቆጣለሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ፊቴን ከእነርሱ እደብቃለሁ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አልረዳቸውም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ይዋጣሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እውጣቸዋለሁ” ወይም “ጠላቶቻቸው እንዲውጡአቸው እፈቅድላቸዋለሁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ተዋጡ

ይህ “ፈጽመው ጠፉ” ለሚለው ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ብዙ ጥፋትና መከራ ያገኛቸዋል

ይህ ጥፋቱንና መከራውን እንደ ሰው መስሎ ይገልጻቸዋል። አ.ት፡ “ብዙ ጥፋትና መከራ ይደርስባቸዋል” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

-- መካከል እነዚህ ጥፋቶች የመጡብን?

ይህ ጥፋቱንና መከራውን እንደ ሰው መስሎ ይገልጻቸዋል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ ንግግር ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “-- መካከል እነዚህ ጥፋቶች እያጠፉኝ ነው” (ሰውኛ እና ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አምላካችን በመካከላችን አይደለም

“ከእንግዲህ እግዚአብሔር እየጠበቀን አይደለም” ወይም “እግዚአብሔር ለብቻችን ትቶናል”

Deuteronomy 31:19

በአፋቸው አኑረው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንዲያሰላስሉትና እንዲዘምሩት አድርጋቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ወተትና ማር የምታፈሰውን ምድር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ብዙ ወተትና ማር የሚፈስባት ምድር” ወይም “ከብት ለማርባትና ለእርሻ ምርጥ የሆነች ምድር” ይህንን በዘዳግም 6፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 31:21

በዚህ ሕዝብ ላይ ብዙ ክፋትና መከራ በመጣባቸው ጊዜ

እዚህ ጋ ክፋትና መከራ ሰብዓዊ ፍጥረት ሆነው ሰዎችን ሊያገኙ የሚችሉ መስለው ተገልጸዋል። አ.ት፡ “ይህ ሕዝብ ብዙ ክፋትና መከራ በሚገጥመው ጊዜ” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

ይህ መዝሙር በፊታቸው እንደ ምስክር ሆኖ ይመሰክርባቸዋል

መዝሙሩ እንደ ሰብዓዊ ፍጥረት ሆኖ በፍርድ ቤት ውስጥ በእስራኤል ላይ እንደሚመሰክር ይናገራል። (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ በዘሮቻቸው አፍ የሚረሳ አይሆንም

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ዘሮቻቸው በአፋቸው ውስጥ መጠበቃቸውን አይረሱም” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ በዘሮቻቸው አፍ የሚረሳ አይሆንም

ይህ በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ዘሮቻቸው በአፋቸው ውስጥ መጠበቅ እንዳለባቸው ያስታውሳሉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ በዘሮቻቸው አፍ የሚረሳ አይሆንም

“በአፋቸው መርሳት” የሚለው የአነጋገር ዘይቤ ስለ እርሱ መናገርን ማቆም ማለት ነው። አ.ት፡ “ዘሮቻቸው ለእርስ በእርሳቸው ስለ እርሱ ከመናገር አያቆሙም”

የሚሠሩትን ዕቅድ

ሰዎች ለማድረግ የሚያቅዱት እርሱ እንደ አካላዊ ቁስ ተደርጎ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “ለማድረግ የሚያቅዱት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ተስፋ የሰጠኋችሁ ምድር

እግዚአብሔር ስለምድሪቱ የሰጠው ተስፋ ለእስራኤል ሕዝብ እንደሚሰጣቸው ነበር። ይህ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እሰጣቸዋለሁ ብዬ ተስፋ የሰጠዃቸው ምድር” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 31:22

ብርቱ ሁን፣ ድፍረትም ይኑርህ

“ብርቱና ደፋር ሁን” ይህንን በዘዳግም 31፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 31:24

በአንተ ላይ ምስክር

ሙሴ እንደ አንድ ሰው አድርጎ ለሌዋውያን ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

Deuteronomy 31:27

አመጸኛና አንገተ ደንዳና ሕዝብህ

ሙሴ እንደ አንድ ሰው አድርጎ ለሌዋውያን ይናገራል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚለው ቃል ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

የአንተ አንገተ ደንዳና

በዘዳግም 9፡6 ላይ “እልኸኛ” የሚለውን እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ከሞትኩኝ በኋላ ይልቁን እንዴት?

ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ ሕዝቡ እንዴት ያሉ አመጸኞች እንደነበሩ አጽንዖት ይሰጣል። ይህ እንደ ንግግር ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እኔ ከሞትኩኝ በኋላ እንኳን በይበልጥ አመጸኛ ትሆናላችሁ” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

እነዚህን ቃላት በጆሮአቸው እንድናገር

እዚህ ጋ “በጆሮአቸው” ማለት ሕዝቡን ራሳችውን ማለት ነው። አ.ት፡ “የዚህ መዝሙር ቃሎች እነግራችው ዘንድ” (See: Synecdoche)

በእነርሱ ላይ ምስክር እንዲሆኑ ሰማይና ምድርን እጠራለሁ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ሙሴ ለሚናገረው ምስክሮች እንዲሆኑ በሰማይና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ይጠራል ወይም 2) ሙሴ እንደ ሰዎች ቆጥሯቸው ለሰማይና ለምድር ይናገራል፣ እርሱ ለሚናገረው ምስክሮች እንዲሆኑም ይጠራቸዋል። ተመሳሳይ ሐረግ በዘዳግም 30፡19 ላይ ይታያል።

ፈጽሞ ራሳችሁን ታረክሳላችሁ

“ሙሉ በሙሉ ስሕተት የሆነውን ታደርጋላችሁ”። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት፡

እኔ ካዘዝኳችሁ መንገድ ዘወር ትላላችሁ

“የሰጠዃችሁን መመሪያ መከተል ታቆማላችሁ”። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 9፡12 እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የሚወክለው የእግዚአብሔርን ውሳኔ ወይም ምዘና ነው። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ውሳኔ ክፉ የሆነ” ወይም “እግዚአብሔር ክፉ ነው ብሎ የሚቆጥረውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእጆቻችሁ ሥራ አማካይነት

እዚህ ጋ “እጆቻችሁ” ማለት ሕዝቡን ራሳቸውን ማለት ነው። አ.ት፡ “በሠራችሁት ሥራ ምክንያት” (See: Synec- doche)

Deuteronomy 31:30

ሙሴ በእስራኤል ጉባዔ ጆሮዎች ሁሉ አሰማ

እዚህ ጋ “ጆሮዎች” የሚያመለክቱት ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ ሁሉ አሰማቸው” (See: Synec- doche)

አሰማ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) “ዘመረ” ወይም 2) “ተናገረ”

የዚህን መዝሙር ቃላት

በውስጠ ታዋቂነት ያለውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እርሱን ያስተማረበትን የመዝሙሩን ቃላት” (See: Ellipsis)


Chapter 32

1 ሰማያት ሆይ፥ አድምጡ እኔም እናገራለሁ፤ ምድር ሆይ፥ አንቺም የአፌን ቃል ስሚ። 2 ትምህርቴም እንደ ዝናብ ይውረድ፤ ቃሌም እንደ ጤዛ ይንጠባጠብ፤ በቡቃያ ሣር ላይ እንደ ካፊያ፥ ለጋ ተክልም ላይ እንደ ከባድ ዝናብ ይውረድ። 3 እኔ የእግዚአብሔርን ስም አውጃለሁ፤ የአምላካችንን ታላቅነት አወድሱ። 4 እርሱ ዐለትና ሥራውም ፍጹም፥ መንገዱም ሁሉ ትክክል ነው። የማይሳሳት ታማኝ አምላክ፤ ቀጥተኛና ጻድቅ አምላክም እርሱ ነው። 5 በእርሱ ላይ ክፋት ፈጽመዋል። ከነውራቸው የተነሣ ከእንግዲህ ልጆቹ አይደሉም። ወልጋዳና ጠማማ ትውልዶች ናቸው። 6 እናንተ ተላላና ጥበብ የጎደላችሁ ሕዝብ፤ለእግዚአብሔር የምትመልሱለት በዚህ መንገድ ነውን? አባታችሁና ፈጣሪያችሁ የሠራችሁና ያበጃችሁእርሱ አይደለምን? 7 የጥንቱን ዘመን፥ የብዙ ዓመቶችን አስታውሱ፤ አባቶቻችሁን ጠይቁ ይነግሩማልም፥ ሽማግሌዎቻችንም ጠይቁ ያስረዱአችኋል። 8 ታላቁ አምላክ ለአሕዛብ ርስታቸውን በሰጠ ጊዜ የሰውንም ዘር በለያየ ጊዜ፤ በእስራኤል ልጆች ቁጥር ልክ፤ የአሕዛብን ርስት ድንበር ለየ። 9 የእግዚአብሔር ድርሻ የገዛ ሕዝቡ ያዕቆብ የተለየ ርስቱ ነውና። 10 እርሱን በምድረ በዳ፤ ባዶና ጭው ባለ በረሓ ውስጥ አግኘው፤እንደ ዐይኑ ብሌን ጠበቀው። 11 ንስር ጎጆዋን እንደትጠብቅ፤ በጫጩቶቿም ላይ እንደምትረብብ፥ እነርሱን ለመያዝ ክንፎቿን እንደምትዘረጋ በክንፎቿም እንደምትሸከማቸው፥ እግዚአብሔር ክንፎቹን ዘርግቶ፥ ተሸከሞ ወሰዳቸው። 12 እግዚአብሔር ብቻ መራው ምንም ባዕድ አምላክ ከእርሱ ጋር አልነበረም። 13 በምድር ከፍታ ላይ አስኬደው፤ የእርሻንም ፍሬ መገበው፤ ከዐለት ድንጋይ ማር አበላው፤ ከባልጩትም ድንጋይ ዘይት መገበው። በወንድና በሴት ልጆቹ ተቆጥቶአልና። 14 የላሙንና የበጉን መንጋ ቅቤና ወትት የሰቡትን በጎችና ፍየሎች፤ የባሳንን ሙኩት በግ፤ መልካም የሆነውንም ስንዴ ማለፊያውንም የወይን ጠጅ ጠጠህ። 15 ይሹሩን ወፈረ፥ ረገጠ፤ ስብ ጠገበ፥ ሰውነቱ ደነደነ፥ ለሰለሰም። የፈጠረውንም አምላክ ተወ፤ የመጠጊያ ዐለት የሆነውን አዳኙንም ናቀው። 16 በባዕዳን አማልክታቸው አስቀኑት፤ በአስፈያፊ ጣዖቶቻቸውም አስቆጡት። 17 አምላክ ላልሆኑ አጋንንት፥ ላላወቋቸው አማልክት፥ ከጊዜ በኋላ ለተነሡ አማልክት፥ አባቶቻችውም ላልፈሯቸው አማልክት ሠዉ። 18 አባት የሆናችሁን ዐለት ከዳችሁት፤ የወለዳችሁን አምላክ ረሳችሁ። 19 እግዚአብሔር ይህን አይቶ ተዋቸው፤ በወንድና በሴት ልጆቹ አስጥተውታልና። 20 እርሱም እንዲህ ብሎአል፦ ፊቴን ከእነርሱ እሰውራለሁ፤ መጨረሻቸው ምን እንደሚሆንም አያለሁ፤ ጠማማ ትውልድ፤ የማይታሙንም ልጆች ናቸውና። 21 አምላክ ላልሆነው አስቀኑኝ፤ በከንቱ ጣዖቶቻቸውም አስቆጡኝ። እኔም ሕዝብ ባልሆነው አስቀናቸዋል፤ በማያስተውልም ሕዝብ አስቆጣቸዋለሁ። 22 በቁጣዬ እሳት ተቀጣጥሎአልና፤እስከ ሲኦል ዘልቆ ይነዳል፤ ምድርን እስከ ሰብሏ ይበላል፤ የተራሮችንም መሠረት ያቀጣጥላል። 23 በመዓት ላይ መዓት አመጣባቸዋለሁ። ፍላጻዬንም በእነርሱ ላይ እተኩሳለሁ። የሚያጠፋ ራብ፤በልቶ የሚጨርስ ቸነፈርና ከባድ መቅሠፍት እሰድባቸዋለሁ፤ 24 የአራዊትን ሹል ጥርስ፥ በምድር የሚሳብ የእባብ መርዝም እሰድባቸዋለሁ። 25 ሰይፍ መንገድ ላይ ያስቀራቸዋል፤ በመኝታቸውም ድንጋጤ ይነግሣል፤ጎልማሳውና ልጃገረዷ፤ ሕፃኑና ሽማግሌው ይጠፋሉ። 26 ከሰዎችም መካከል መታሰቢያቸውን አጠፋለሁ፥ እበትናቸዋለሁም፤አልሁ፤ 27 ድል ያደረገው እጃችን ነው ብለው፥ ጠላቶቻቸው በስሕተት እንዳይታበዩ፥ የጠላት ማስቆጣት እንዳይሆን እሠጋለሁ። 28 እስራኤላውንም አእምሮ የጎደላቸው፤ ማስተዋልም የሌላቸው ናቸው። 29 አስተዋዮች ቢሆኑ ኖሮ ይህን በተገነዘቡና መጨረሻቸው ምን እንደሚሆን ባስተዋሉ ነብር። 30 መጠጊያ ዐለታቸው ካልሸጣቸው እግዚአብሔር ካልተዋቸው በቀር፥ አንድ ሰው እንዴት ሺሁን ያሳድዳል፥ ሁለቱስ እንዴት አሥር ሺሁን እንዲሸሹ ያደጋሉ? 31 የእነርሱ መጠጊያ ዐለታቸው እንደ እኛ መጠጊያ ዐለት አለመሆኑን፤ ጠላቶቻችንም እንኳ አይክዱም። 32 ወይናቸው ከሰዶም ወይን ከገሞራም እርሻ ይመጣል፤ የወይናቸው ፍሬ በመርዝ፥ ዘለላቸውም መራራ ነው። 33 ወይናቸው የእባብ መርዝ፤ መርዙም የጨካኝ እባብ ነው። 34 ይህስ በእኔ ዘንድ ተጠብቆ ያለ፤ በመዝገቤስ የታተመ አይደለምን? 35 በቀል የእኔ ነው፤ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ፥ ጊዜው ሲደርስ እግራቸው ይሰናከላል፤ የመጥፊያቸው ቀን ቀርቦአል፤ የሚመጣባቸውም ነገሮች ይፈጥንባቸዋል። 36 ኃይላቸው መድከሙን ባሪያም ሆነ ነጻ ሰው አለመቅረቱን በሚያይበት ጊዜ፤ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ይፈርዳል፤ ለአገልጋዮቹም ይራራል። 37 እንዲህም ይላል፦ መጠጊያ ዐለት የሆኗቸው፤ አማልክታቸው ወዴት አሉ? 38 የመሥዋዕታቸውን ስብ የበሉ፤ የመጠጥ ቁርባናችውንም የወይን ጠጅ የጠጡ አማልክት ወዴት ናቸው? እስቲ ይነሡና ይርዷችሁ! እስቲ መጠለያ ይስጧችሁ! 39 እኔ ራሴ እርሱ እንደ ሆንሁ እዩ፤ ከእኔም በቀር ሌላ አምላክ የለም፤እገድላለሁ፤ አድናለሁ፤አቆስላለሁ፤ እፈውሳለሁም፤ ከእጄም የሚያስጥል ማንም የለም። 40 እጄን ወደ ሰማይ አነሣለሁ፤ ለዘላለምም ሕያው እንደ ሆንሁ እናገራለሁ።። 41 የሚያብራቀርቅ ሰይፌን ስዬ እጄ ለፍርድ ስይዘው፤ ባላጋራዎቼን እበቀላቸዋለሁ፤ ለሚጠሉኝም እንደሥራቸው እከፍላቸዋለሁ። 42 ሰይፌ ሥጋ በሚበላበት ጊዜ፥ ፍላጾቼ በደም እንዲሰክሩ አደርጋለሁ፤ ደሙ የታረዱትና የምርኮኞች የጠላት አለቆችም ራስ ደም ነው። 43 አሕዛብ ሆይ ከሕዝቡ ጋር ደስ ይበላችሁ፤ እርሱ የአገልጋዮቹን ደም ይመልሳል፤ጠላቶቹንም ይበቀላል። ምድሪቱንና ሕዝቡን ይቤዣቸዋል። 44 ሙሴም ከነዌ ልጅ ከኢያሱ ጋር መጥቶ የመዝሙር ቃሎችን በሕዝቡ ጆሮ ተናገረ። 45 ሙሴም እነዚህን ቃሎች ሁሉ ለመላው እስራኤል ተናገሮ ጨረሰ። 46 እርሱም እንዲህ አላቸው፦ የዚህን ሕግ ቃሎች ሁሉ በጥንቃቄ ይጠብቁ ዘንድ ልጆቻችሁን እንድታዟቸው እኔ ዛሬ በግልጥ የምነግራችሁን ቃሎች ሁሉ በልባችሁ አኑሩ። 47 ቃሎቹ ለእናንተ ሕይወታችሁ ናቸው፥ ባዶ ቃሎች አይደሉም፥ በእነርሱ ዮርዳንስን ተሻገራችሁ በምትወርሷትም ምድር ረጅም ዘመን ትኖራላችሁ። 48 በዚያችም ዕለት እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረ፦ 49 ከኢያሪኮ ማዶ ባለው የሞዓብ ምድር ከዓብሪም ተራሮች አንዱ ወደ ሆነው ወደ ናባው ተራራ ወጥተህ ለእስራኤላውያን ርስት አድርጌ የምሰጣትን የከነዓን ምድር አሻግረህ ተመልከት። 50 ወንድምህ አሮን በሖር ተራራ ላይ እንደ ሞተና ወደ ወገኖቹ እንደ ተስበስበ ሁሉ አንተም በወጣህበት በዚያ ተራራ ላይ ሙት፤ ወደ ወገኖችህም ተሰብሰብ። 51 ይህ የሚሆንበት ምክንያት ሁለታችሁም በሲን ምድረ በዳ በቃዴስ በምሪባ ውሃ አጠገብ በእስራኤላውያን መካከል በእኔ ላይ ባለመታመናችሁ፤ እንዲሁም በእስራኤላውያን መካከል የሚገባውን አክብሮት ባለመስጠታችሁ ነው። 52 ስለዚህ ምድሪቱን ከሩቅ ሆነህ ታያታለህ እንጂ ለእስራኤል ሕዝብ ወደምሰጣት ምድር አትገባም።



Deuteronomy 32:1

እናንተ ሰማያት ጆሮአችሁን ስጡ -- ምድርም ትስማ

እዚያ ሆነው ይሰሙ ይመስል እግዚአብሔር ለሰማያትና ለምድር ይናገራል። ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) እግዚአብሔር የሚናገረው በሰማይና በምድር ለሚኖሩት ነው፤ ወይም 2) እግዚአብሔር እንደ ሰው ቆጥሯቸው ለሰማይና ለምድር ይናገራል። (See: Apostrophe)

ትምህርቴ እንደ ዝናብ ይንጠባጠብ፣ በተክሎች ላይ እንደጎርፍ

ይህ ማለት የእርሱን ጠቃሚ ትምህርት ሕዝቡ በትጋት እንዲቀበሉ እግዚአብሔር ይፈልጋል። (See: Simile)

የተጣራ

ጤዛ የሚታይበትን ሂደት የሚገልጽ ቃል በራስህ ቋንቋ ተጠቀም።

ጠል

ቅዝቃዜ ባለበት ጠዋት በቅጠሎችና በሣር ላይ የሚገኝ ውሃ

ለጋ ሣር

“አዲስ ተክሎች”

መጉረፍ

ከባድ ዝናብ

Deuteronomy 32:3

የእግዚአብሔርን ስም ዐውጅ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር መልካም መሆኑን ተናገር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የአምላካችንን ታላቅነት አሳስቡ

“አምላካችን ታላቅ መሆኑን ሰዎች ማወቃቸውን አረጋግጡ”

ዐለቱ

ይህ እንደ ዐለት ብርቱ እና ሕዝቡን መጠበቅ ለሚችለው ለእግዚአብሔር ሙሴ የሰጠው የተፀውዖ ስም ነው። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሥራው

“እርሱ የሚያደርገው ሁሉ”

መንገዶቹ ሁሉ ትክክል ናቸው

መንገድ ላይ መራመድ አንድ ሰው ሕይወቱን እንዴት እንደሚኖረው የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ሁሉንም ነገር በትክክለኛ መንገድ አድርጓል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እርሱ ትክክለኛና ቀጥተኛ ነው

እነዚህ ሁለት ቃላት በመሠረቱ የሚሉት አንድ ነገር ሆኖ እግዚአብሔር ፍትሐዊና ትክክለኛውን ነገር እንዳደረገ አጽንዖት ይሰጣሉ። (See: Doublet)

Deuteronomy 32:5

በእርሱ ላይ በእርኩሰት አድርገዋል

“ትክክል ያልሆነን ነገር በማድረግ ተቃወሙት”። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ወልጋዳና ጠማማ ትውልድ

“ወልጋዳ” እና “ጠማማ” የሚሉት ቃላት በመሠረቱ ትርጉማቸው አንድ ነው። ሙሴ ትውልዱ ምን ያህል ክፉ እንደሆነ አጽንዖት ለመስጠት ይጠቀምባቸዋል። አ.ት፡ “ፈጽሞ ክፉ የሆነ ትውልድ” (See: Doublet)

-ሕዝብ ለእግዚአብሔር በዚህ መንገድ ትመልስለታለህ?

ሙሴ ሕዝቡን ለመገሰጽ ይህንን ጥያቄ ይጠቀማል። አ.ት፡ “-ሕዝብ፣ ለእግዚአብሔር ተገቢውን ምስጋና ማቅረብ አለባችሁ” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አንተ ሞኝና የማትረባ ሕዝብ

“ሞኝ” እና “የማትረባ” የሚሉት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም ያላቸው ሲሆኑ ሕዝቡ እግዚአብሔርን ባለመታዘዛቸው ምን ያህል ሞኞች እንደሆኑ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “እጅግ ሞኞች የሆናችሁ ሰዎች” (See: Doublet)

አባትህ -- ፈጥሮሃል -- ሠርቶሃል፣ አጽንቶሃል

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት ቃላት እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥሮች ናቸው።

የፈጠረህ አባትህ አይደለምን?

ሙሴ ሕዝቡን ለመገሰጽ በጥያቄ መልክ ይጠቀማል። ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ ንግግር ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የፈጠረህ አባትህ ነው” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:7

ትዝ ይበልህ -- አስብ -- አባትህ -- ያሳዩሃል -- ሽማግሌዎችህ -- ይነግሩሃል

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚሉት ቃላት እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

ትዝ ይበልህ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አስታውስ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የጥንቱን ዘመን

“ከረጅም ዓመታት በፊት”። ሙሴ፣ የእስራኤል ቅድመ ቅድም አያቶች ይኖሩ የነበሩበትን ጊዜ ያመለክታል።

ከብዙ ዓመታት በፊት ስለነበረው ጊዜ አስብ

ይህ ቀደም ሲል በነበረው ክፍል ሙሴ ተናግሮት የነበረው ድጋሚ ነው። ሙሴ የእስራኤል ሕዝብ እንደ ሕዝብ በታሪካቸው ላይ እንዲያተኩሩ ይፈልጋል። (See: Parallelism)

ያሳይሃል

“ግልጽ ያደርግልሃል” ወይም “እንድታስተውለው ያስችልሃል”

ለሕዝቡ ርስታቸውን ሰጣቸው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ሕዝቡ ሊኖሩ በሚገባቸው ስፍራ ላይ አስቀመጣቸው”። “ርስት አድርጎ ወደሚሰጣችሁ” የሚሉ ተመሳሳይ ቃላት በዘዳግም 4፡21 ላይ ይታያሉ። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ደግሞም የአማልክታቸውን ቁጥር በሚወስኑበት ጊዜ ለሕዝቦች ድንበሮችን አደረገላቸው

እግዚአብሔር እያንዳንዱን የሕዝብ ወገን ከአማልክቱ ጋር በራሱ ግዛት እንዲኖር ወስኗል። በዚህ መንገድ የሕዝብ ወገኖችን ጣዖታት ተጽዕኖ ገድቧል።

Deuteronomy 32:9

የእግዚአብሔር ድርሻው ሕዝቡ ነውና፤ ያዕቆብ የርስቱ ዕድል ፈንታው ነው

እነዚህ ሁለት ሐረጎች የሚናገሩት በመሠረቱ አንድ ነገር ነው፣ ስለሆነም ሊጣመሩ ይችላሉ። አ.ት፡ “የያዕቆብ ዘሮች የእግዚአብሕር ርስት ናቸው” (See: Parallelism)

አገኘው -- ጋረደውና ተጠነቀቀለት -- ጠበቀው

“ያዕቆብን አገኘው -- ጋረደውና ተጠነቀቀለት -- ጠበቀው”። ይህንን ምናልባት ሙሴ እንደ ብዙ ሕዝብ አድርጎ የሚናገረው ስለ እስራኤላውያን እንደሆነ መተርጎም ያስፈልግህ ይሆናል። አ.ት፡ “ቅድመ ቅድም አያቶቻችንን አገኛቸው -- ጋረዳቸውና ተጠነቀቀላቸው -- ጠበቃቸው”

ጭው ባለ ምድረ በዳ

እዚህ ጋ “ጭው ያለ” የሚያመለክተው ባዶ መሬት ላይ ነፋሱ ሲነፍስ የሚያሰማውን ድምፅ ነው።

እንደ ዕይኑ ብሌን ጠበቀው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። የዐይን ብሌን የሚያመለክተው አንድ ሰው ለማየት የሚያስችለውን በዐይኑ ኳስ ውስጥ ያለውን ጥቁሩን ክፍል ነው። ይህ በጣም አስፈላጊና ጥንቃቄ የሚፈልግ የሰውነት ክፍል ነው። ይህ ማለት የእስራኤል ሕዝብ ለእግዚአብሔር በጣም አስፈላጊና እርሱ ጥበቃ የሚያደርግለትም ነው። አ.ት፡ “በጣም ዋጋ እንዳለውና ውድ ነገር ጠብቆታል”(የአነጋገር ዘይቤ እና Simile የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:11

ንስር ጎጆዋን እንደምትጠብቅና በጫጩቶችዋ ላይ እንደምትሰፍፍ እግዚአብሔር ክንፎቹን ዘርግቶ ወሰዳቸው፣ በላባዎቹም ተሸከማቸው

ይህ ማለት እስራኤላውያን በበረሃ እያሉ እግዚአብሔር ጠብቋቸዋል፣ ተከላክሎላቸዋልም። (See: Simile)

ላባዎች

የወፍ የክንፉ ውጫዊ ጫፍ

መራው -- ከእርሱ ጋር

ሙሴ እንደገና እስራኤላውያንን “ያዕቆብ” በማለት ይናገራል (ዘዳግም 32፡9-10)። ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ ብዙ ሕዝብ አድርጎ እንደተናገራቸው መተርጎም ያስፈልግህ ይሆናል። አ.ት፡ “መራቸው -- ከእነርሱ ጋር”

Deuteronomy 32:13

በምድሪቱ የከፍታ ስፍራ ላይ አስኬደው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። “እርሱን” የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በምድሪቱ የከፍታ ስፍራዎች ላይ አስኪዷቸዋል” ወይም “ምድሪቱን እንዲወስዱና እንዲሰፍሩባት እግዚአብሔር ረድቶአቸዋል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

አስኬደው -- መገበው -- አጠገበው

ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ “ያዕቆብ” በመቁጠር መናገሩን ይቀጥላል (ዘዳግም 32፡9-10)። ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ ብዙ ሕዝብ አድርጎ እንደተናገራቸው መተርጎም ያስፈልግህ ይሆናል። “አባቶቻችንን እንዲሄዱ አደረጋቸው -- መገባቸው -- አጠገባቸው” (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

የእርሻውን ፍሬ መገባቸው

“የሚበላው ብዙ ሰብል ወዳለበት ምድር አመጣው”

ከዐለቱ በሚወጣ ማርና ከባልጩታማ ቋጥኝ በሚገኝ ዘይት አጠገበው

ምድሪቱ በዐለት ቀዳዳዎች ውስጥ ማር የሚሠሩ ብዙ የጫካ ንቦች ነበሯት። በተጨማሪም፣ በዐለቶች፣ በኮረብቶችና በተራራዎች ላይ የሚበቅሉ ዘይት የሚሰጡ ብዙ የወይራ ዛፎች ነበሩ።

በማር አጠገበው

ይህ ልክ እናት ለሕፃን ልጇ ጡቷን እንደምትሰጠው ዓይነት ነው። “ማር እንዲጠባ ፈቀደለት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:15

ይሹሩን

ሙሴ በሚገባ እንደ ተቀለበና ባለቤቱ ይሹሩን ብሎ እንደሰየመው እንስሳ ስለ እስራኤላውያን ይናገራል። “ ’ይሹሩን’ ማለት ‘ቀጥተኛ የሆነ’ ማለት ነው” የሚል የግርጌ ማስታወሻ ልትጨምርበት ትችላለህ። የአንተ ቋንቋ እስራኤላውያንን እንደ ይሹሩን የማይገልጻቸው ከሆነ የተከፈተው ተለዋዋጭ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንደሚያደርገው እስራኤላውያንን እንደ ብዙ ሕዝብ ማመልከት ትችላለህ። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

መስባቱን ቀጠለ፣ ረገጠም

በሚገባ የተቀለበው እንስሳ፣ ገር ከመሆን ይልቅ የሚራገጠው ይሹሩን እግዚአብሔር ቢንከባከባቸውም እንኳን ያመጹትን እስራኤላውያንን የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መስባትህን ቀጠልክ፣ በጣም ሰብተህ ነበር፣ ፍጆታህን በልተህ ነበር

ሙሴ ለይሹሩን በሚዘምረው መዝሙር እስራኤላውያንን ይገስጻቸዋል። “ሰባችሁ፣ በጣምም ሰባችሁ፣ የሚቻላችሁን ያህልም ሰባችሁ”

የድነቱን ዐለት

ይህ ማለት እግዚአብሔር እንደ ዐለት ብርቱ ነው፣ ሕዝቡን ለመጠበቅም ይችላል ማለት ነው። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዐለቱ

ይህ ሙሴ ለእግዚአብሔር የሚሰጠው የተጸውዖ ስም እንደ ዐለት ብርቱና ሕዝቡን ለመጠበቅ የሚችል ነው። ይህንን በዘዳግም 32፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔርን አስቀኑት

እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አስቀኑት።

Deuteronomy 32:17

ሠዉ

“የእስራኤል ሕዝብ ሠዉ”

በቅርቡ የመጡትን አማልክት

ይህ ማለት እስራኤላውያን ስለ እነዚህ አማልክት የተማሩት በቅርቡ ነው።

አባቶችህ

ሙሴ ለእስራኤላውያን እንደ ብዙ ሰው ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “የአንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

አባትህን -- ትተሃል -- ረስተሃል -- ሰጥቶሃል

ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” እና “የአንተ” የሚልበት አገባብ ሁሉ ብዙ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

ዐለቱን ትተሃል

እዚህ ጋ እግዚአብሔር ብርቱና መከላከያ ስለሆነ ዐለት ተብሎ ተጠርቷል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔርን የመከላከል ክብካቤ ትተሃል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዐለቱ

ይህ ሙሴ ለእግዚአብሔር የሚሰጠው የተጸውዖ ስም እንደ ዐለት ብርቱና ሕዝቡን ለመጠበቅ የሚችል ነው። ይህንን በዘዳግም 32፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አባትህ የሆነውን -- ልጅ የሰጠህን

ይህ እግዚአብሔርን ከአባትና ከእናት ጋር ያነጻጽራል። ይኸውም፣ እግዚአብሔር በሕይወት እንዲኖሩና ሕዝብ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “አባት ያደረጋችሁ … ሕይወትን የሰጣችሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:19

ወንዶችና ሴቶች ልጆቹ

ይህ እግዚአብሔር ሕይወትን የሰጣቸውንና ሕዝብ ያደረጋቸውን የእስራኤልን ሕዝብ ያመለክታል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ፊቴን ከእነርሱ እደብቃለሁ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ከእነርሱ እርቃለሁ” ወይም “እነርሱን መርዳቴን አቆማለሁ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

መጨረሻቸው ምን እንደሚሆን አያለሁ

“የሚደርስባቸውን አያለሁ”

Deuteronomy 32:21

እኔን አስቀንተውኛል

እዚህ ጋ “እኔን” የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ነው።

አምላክ ያልሆነውን

“ሐሰተኞች አማልክትን”

የማይጠቅሙ ነገሮች

“ነገሮች” ምን እንደሆኑ ግልጽ ማድረግ ይኖርብህ ይሆናል። አ.ት፡ “የማይጠቅሙ ጣዖታት” (See: Assumed Knowl- edge and Implicit Information)

እነዚያን ሕዝብ ያልሆኑትን

“የአንድ ሕዝብ ወገን ያልሆኑ ሰዎች”

ሞኝ ሕዝብ

“ሞኝ” የሚለውን በዘዳግም 32፡6 እንዳለው አድርገህ ተርጉመው።

Deuteronomy 32:22

በቁጣዬ እሳት ተለኩሷልና -- የተራሮች መሠረቶች

እግዚአብሔር ቁጣውን ከእሳት ጋር ያነጻጽረዋል። ይህ የሚያስቆጣውን በሚያጠፋበት ኃይሉ ላይ አጽንዖት ያደርጋል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በቁጣዬ እሳት ተለኩሶ ነዶአል -- ይውጣል -- ተቀምጧል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስለ ተቆጣሁ እሳት መለኮስ ጀምሬአለሁ፣ ይውጣል . . . የሚያጠፋ ነው . . . ተቀምጧል” ወይም “በምቆጣበት ጊዜ ጠላቶቼን እንደ እሳት አጠፋለሁ፣ በምድርና በ . . . ያለውን ሁሉ አጠፋለሁ . . . እውጣለሁ . . . አስቀምጣለሁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እስከ ጥልቁ ሲዖል

“እስከ ሙታን ዓለም ድረስ”

Deuteronomy 32:23

ጥፋትን እከምርባቸዋለሁ

በእስራኤላውያን አናት ላይ የሚቆልላቸው ቆሻሻዎች የሆኑ በሚመስል መልኩ በእስራኤላውያን ላይ ስለሚደርስባቸው መጥፎ ነገሮች እግዚአብሔር ይናገራል። አ.ት፡ “ብዙ መጥፎ ነገሮች እንደሚደርሱባቸው አረጋግጣለሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ፍላጻዎቼን ሁሉ በእነርሱ ላይ እወነጭፋቸዋለሁ

እዚህ ጋ እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ላይ በእርግጠኝነት እንዲደርስባቸው የሚያደርጋቸውን መጥፎ ነገሮች አንድ ሰው በቀስቱ ፍላጻዎችን ከማስወንጨፉ ጋር ያነጻጽራል። አ.ት፡ “እነርሱን ለመግደል ማድረግ የምችለውን ሁሉ አደርጋለሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በረሀብ ያልቃሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። የነገር ስም የሆነው “ረሀብ” “ይራባሉ” ወደሚል ግሥ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ይዝላሉ፣ በመራባቸው ምክንያትም ይሞታሉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ እና የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

እነርሱ -- ረሀብ እና በሚያቃጥል ሙቀትና በአሰቃቂ ጥፋት ይዋጣሉ

“የሚያቃጥል እሳት” ለሚለው ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) እስራኤላውያን በንዳድ ይሰቃያሉ ወይም 2) በድርቅ ወይም በረሀብ ወቅት የአየሩ ሁኔታ ባለተለመደ መልኩ ሞቃት ይሆናል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እነርሱ . . . ረሀብ፣ የሚያቃጥል ሙቀትና አሰቃቂ ጥፋት ይውጣቸዋል” ወይም “እነርሱ . . . ረሀብ፣ በሚያቃጥል ሙቀትና በአሰቃቂ ጥፋት ይሞታሉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የዱር አራዊትን ጥርስ፣ አፈር ላይ ከሚሳቡ ነገሮች መርዝ ጋር እልክባቸዋለሁ

ጥርስና መርዝ እንስሳው እነዚህን ነገሮች በመጠቀም የሚገድልባቸው ናቸው። አ.ት፡ “እንዲነክሷቸው የዱር አራዊትን፣ ነክሰው እንዲመርዟቸው በአፈር ላይ የሚሳቡትን ነገሮች እልካለሁ” (See: Synecdoche)

Deuteronomy 32:25

ሰይፍ በውጭ ያስቀራቸዋል

እዚህ ጋ “ሰይፍ” የሚወክለው የጠላትን ሰራዊት ነው። አ.ት፡ “እስራኤላውያን ውጪ በሚሆኑበት ጊዜ የጠላት ሰራዊት ይገድላቸዋል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ድንጋጤ ያደርጋል

x

Deuteronomy 32:27

የጠላትን ትንኮሳ ያልሰጋሁ ብሆን ኖሮ

“የጠላትን ትንኮሳ ሰግቼ ነበር”

የጠላት ትንኮሳ

ይህ የነገር ስም እንደ ግሥ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ጠላት እንዳይተነኩሰኝ” ወይም “ጠላት እንድቆጣ እንዳያደርገኝ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ጠላት

እግዚአብሔር የእርሱን ጠላቶች እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “ጠላቴን” ወይም “ጠላቶቼን” (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

በስሕተት መፍረድ

“አሳስቶ መረዳት”

እጃችን ከፍ ከፍ ብሏል

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው የሰውን ጉልበት ወይም ኃይል ነው። ከፍ ከፍ ማለት ጠላትን የማሸነፍ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እኛ ይበልጥ ኃይለኞች በመሆናችን አሸንፈናቸዋል” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:28

ምነው ጥበበኞች በሆኑ፣ ይህንን ያስተውሉ ዘንድ፣ የሚመጣባቸውን ፍርድ ያውቁ ዘንድ

ሙሴ እውነት እንዲሆኑ የሚመኛቸውን አንዳንድ ነገሮች ይናገራል፤ ይሁን እንጂ ጥበበኞች እንዳልሆኑና አለመታዘዛቸው እግዚአብሔር ይህንን ጥፋት እንዲያመጣባቸው እንደሚያደርገው እንዳልተገነዘቡ ያውቃል። (See: Hypothetical Situations)

የሚመጣባቸው ፍርድ

የነገር ስም የሆነው “ፍርድ” እንደ ግሥ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በእነርሱ ላይ ሊደርስባቸው ያለ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:30

እግዚአብሔር አሳልፎ ካልሰጣቸው -- አንዱ አንድ ሺህ ማሳደድ እንዴት ይችላል

ሙሴ ጠላቶቻቸው ለምን እንዳሸነፏቸው ለማስተዋል ጥበበኞች ስላለመሆናቸው ጥያቄን በመጠቀም ሕዝቡን ይገስጻቸዋል። ይህ ጥያቄ ክፍት በሆነው ተለዋዋጭ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ውስጥ እንዳለው መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አንዱ አንድን ሺህ እንዴት ሊያሳድድ ይችላል፣ ሁለቱ አሥር ሺዎችን እንዲሸሹ ማድረግ እንዴ ይቻላቸዋል?

በውስጠ ታዋቂነት ያለውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “1 የጠላት ወታደር የእናንተን 1000 ሰዎች እንዴት ሊያሳድድ ቻለ፣ 2 የጠላት ወታደሮችስ የእናንተን 10000 ሰዎች እንዲሸሹ ለማድረግ እንዴት ቻሉ” (See: Numbers and Ellipsis)

Deuteronomy 32:32

ወይናቸው ከሰዶም ወይን ይመጣልና -- ዘለላቸው መራራ ናቸው

ሙሴ ሐሰተኛ አማልክት የሚያመልኩ ጠላቶችን በሰዶም ገሞራ ከኖሩት ክፉ ሕዝቦች እና መርዛማ ፍሬ ከሚያፈሩ የወይን ሐረጎች ጋር ያነጻጽራቸዋል። ይህ ማለት እስራኤላውያን በዙሪያቸው እንዳሉት ሕዝቦች ለማድረግ ከጀመሩ ጠላቶቻቸው ክፉዎች ስለሆኑ እስራኤላውያንን ለሞት ያበቋቸዋል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወይናቸው ከሰዶም ወይን እና ከገሞራም እርሻ ይመጣል

ወይን ለሕዝብ ወገን ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። “ወይናቸው በሰዶምና ገሞራ ይበቅል የነበረው ወይን ቅርንጫፉ ነው” ወይም አ.ት፡ “በሰዶምና ገሞራ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች እንዳደረጉት በተመሳሳይ መንገድ ክፉ ያደርጋሉ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዘለላዎቻቸው

“የወይን ዘለላዎቻቸው

Deuteronomy 32:33

ወይናቸው የእባብ መርዝና የትናንሽ መርዘኛ እባቦች ጨካኝ መርዝ ነው

ሙሴ የእስራኤል ሕዝብን ጠላቶች መርዘኛ ፍሬና ወይን ከሚያበቅል የወይን ሐረግ ጋር ማነጻጸሩን ይቀጥላል። ይህ ማለት ጠላቶቻቸው ክፉዎች ናቸው። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ትናንሽ መርዘኛ እባቦች

መርዘኛ እባቦች

ይህ ዕቅድ በእኔ በምስጢርነት የተጠበቀ፣ በሀብቴም መካከል ታትሞበት የተቀመጠ አይደለምን?

ይህ ጥያቄ እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ ያለው ዕቅድ ዋጋ እንዳለው ሀብት በምስጢር እንደተጠበቀ አጽንዖት ይሰጣል። ምላሽ የማይፈልገው ጥያቄ እንደ ንግግር ተደርጎ ሊተረጎም ይችላል። ደግሞም፣ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ለእስራኤል ሕዝብና ለጠላቶቻቸው ለማድረግ ያቀድኩትን እኔ አውቃለሁ፣ አንድ ሰው ዋጋ ባላቸው ንብረቶቹ ላይ እንደሚቆልፍባቸው በእነዚያ ዕቅዶች ላይ ቆልፌባቸዋለሁ” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:35

በቀል እኔ የምሰጠው ነው፣ ብድራትንም

“በቀል” እና “ብድራትንም” የሚሉት ቃላት በመሠረቱ ትርጉማቸው ተመሳሳይ ነው። አ.ት፡ “እኔ እበቀላለሁ፣ የእስራኤልንም ጠላቶች እቀጣለሁ” (See: Doublet)

ብድራት

አንድ ሰው ስላደረገው ነገር ቅጣት ወይም ሽልማት

እግራቸው ይሰናከላል

መጥፎ የሆነ ነገር ደርሶባቸዋል። አ.ት፡ “ተስፋ የላቸውም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ለእነርሱ የጥፋት ቀን

“እነርሱን የማጠፋበት ጊዜ”

በእነርሱ ላይ ሊመጡባቸው ያሉ ነገሮች በቶሎ ሊደርሱባቸው ይቸኩላሉ

ሊቀጡአቸው በትጋት የሚሮጡ ሰዎችን በሚመስሉበት መልኩ እግዚአብሔር በጠላቶቹ ላይ ሊመጡ ስላሉት መጥፎ ነገሮች ይናገራል። አ.ት፡ “ፈጥኜ እቀጣቸዋለሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:36

እግዚአብሔር ለሕዝቡ ፍትሕን ይሰጣልና

የነገር ስም የሆነው “ፍትሕ” እንደ ቅጽል ወይም ተውሳከ ግሥ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ለሕዝቡ ፍትሐዊ የሆነውን ነገር ያደርግላቸዋል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ለአገልጋዮቹ ይራራል

“አገልጋዮቹን መርዳት እንዳለበት ይሰማዋል”

Deuteronomy 32:37

መጠጊያ ያደረጉ ዐለት፣ አማልክታቸው የት አሉ?

ከሌሎች አማልክት ከለላ ስለመፈለጋቸው የእስራኤልን ሕዝብ እግዚአብሔር ይገስጻቸዋል። ይህ ጥያቄ እንደ ንግግር ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ተመልከቱ፣ እስራኤላውያን እንደሚጠብቋቸው ያሰቧቸው አማልክት ሊረዷቸው አልመጡም” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የመሥዋዕቶቻቸውን ስብ የበሉ እና የመጠጥ ስጦታ የሆነውን ወይን የጠጡ አማልክት

እዚህ ጋ ለሌሎች አማልክት መሥዋዕት በማቅረባቸው የእስራኤልን ሕዝብ እግዚአብሔር ይገስጻቸዋል። ይህ ጥያቄ እንደ ንግግር ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እስራኤላውያን ሥጋና ወይን ያቀረቡላቸው አማልክት ሊረዷቸው አልመጡም” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ይነሡና ይርዷችሁ፤ ከለላ ይሁኗችሁ

በእስራኤላውያን ላይ ለማፌዝ እግዚአብሔር ይህንን ይናገራል። እነዚህ አማልክት ሊረዷቸው እንደማይችሉ ያውቃል። አ.ት፡ “እነዚህ ጣዖታት ሊነሡና ሊረዱ ወይም ሊጠብቋችሁ አይችሉም” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:39

እኔ፣ እኔ እንኳን

“እኔ፣ እኔ ራሴ” ወይም “እኔ፣ እኔ ብቻዬን”። እግዚአብሔር እርሱ ብቻ አምላክ መሆኑን አጽንዖት ለመስጠት “እኔ”ን ይደጋግማል።

እጄን ወደ ሰማይ አንሥቼ እናገራለሁ

“እጄን ወደ ሰማይ አንሥቼ እምላለሁ” ወይም “ምያለሁ”። እጅን ማንሣት የመማል ምልክት ነው።

ለዘላለም እንደምኖር

“ለዘላለም መኖሬ እርግጥ የመሆኑን ያህል” ወይም “ማለቂያ በሌለው ሕይወቴ እምላለሁ”። በዘዳግም 32፡41-42 የተናገረው እንደሚፈጸም ይህ አነጋገር እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያረጋግጣል።

Deuteronomy 32:41

አብረቅራቂ ሰይፌን በምስልበት ጊዜ

“አንጸባራቂውን ሰይፌን በምስልበት ጊዜ”። ይህ ማለት እግዚአብሔር በጠላቶቹ ላይ ለመፍረድና ለመቅጣት ተዘጋጅቷል ማለት ነው። አ.ት፡ “በጠላቶቼ ላይ ለመፍረድ በምዘጋጅበት ጊዜ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እጄ ፍትሕን ማምጣት በሚጀምርበት ጊዜ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ሙሉውን ሰው ነው (See: Synec- doche)

Deuteronomy 32:42

ፍላጻዎቼ በደም እንዲሰክሩ አደርጋቸዋለሁ፣ ሰይፌም ከደም ጋር ሥጋን ይበላል

ፍላጻዎች ሰው የሆኑና የሚያሰክር መጠጥ ይሰጣቸው ይመስል እግዚአብሔር ስለ ፍላጻዎቹ ይናገራል፣ ሰይፉም ስለ ራበው ደሙ ተንጠፍጥፎ ያልወጣለትን እንስሳ እንደሚበላ ሰው መስሎ ይናገራል። እነዚህ ዘይቤአዊ አነጋገሮች ብዙ ጠላቶችን ለመግደል ፍላጻዎችንና ሰይፍን የሚጠቀምን ወታደር የሚያመለክቱ ፈሊጣዊ አነጋገሮች ናቸው። ይህ በተራው እግዚአብሔር በጦርነት ውስጥ ጠላቶቹን ስለመግደሉ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው።(ዘይቤአዊ አነጋገር፣ ፈሊጣዊ አነጋገር እና ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

የጠላት አለቆች ከሆኑት ራስ

ሊሆን የሚችለው ትርጉም “በራሳቸው ላይ ረጅም ጸጉር ካላቸው ጠላቶች” የሚለው ነው።

Deuteronomy 32:43

እናንተ ሕዝቦች ደስ ይበላችሁ

ሙሴ በዚያ ኖረው ይሰሙት ይመስል በየሀገራቱ ሁሉ ለሚኖሩ ሰዎች ይናገራል። (See: (ፈሊጣዊ አነጋገር እና Apostrophe የሚለውን ተመልከት))

የአገልጋዮቹን ደም ይበቀላልና፤ በጠላቶቹ ላይ በቀልን ይመልስባቸዋል

እዚህ ጋ “የአገልጋዮቹን ደም” የሚወክለው የተገደሉትን የእርሱን ንጹሕ አገልጋዮች ሕይወት ነው። አ.ት፡ “አገልጋዮቹን የገደሉትን ጠላቶቹን ይበቀላቸዋል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:44

ነገራቸው -- መናገር

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) “ተናገረ . . . መናገር” ወይም 2) “ዘመረ . . . መዘመር” ናቸው።

በሕዝቡ ጆሮ

x

Deuteronomy 32:46

ተናገራቸው

“ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ ተናገራቸው”

በልባችሁ አኑሩት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ለ -- ትኩረት ስጡ” ወይም “ስለ -- አስቡ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

መስክሬላችኋለሁ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ባይታዘዙ እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ላይ ምን እንደሚያደርግባቸው የተናገረውን ለማመልከት “መስክሬላችኋለሁ” ማለቱን ያመለክታል ወይም 2) እንዲያደርጉት እግዚአብሔር ያዘዛቸውን ለማመልከት “አዝዥችኋለሁ” የሚሉት ናቸው

ልጆቻችሁ

“ልጆቻችሁና ተወላጆቻችሁ”

ይህ ነው

“ይህ ሕግ ነው”

አላስፈላጊ ነገር አይደለም

ይህ ምጸት በአዎንታዊነት ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በጣም ጠቃሚ የሆነ ነገር” (ምጸት የሚለውን ተመልከት)

እርሱ ሕይወትህ ስለሆነ

የነገር ስም የሆነው “ሕይወት” “መኖር” ወደሚል ግሥ ሊተረጎም ይችላል። ሕግን ራሱን የሚወክለውን የመታዘዝን ፈሊጣዊ አነጋገር ግልጽ ማድረግ ይኖርብህ ይሆናል። አ.ት፡ “ብትታዘዝው በሕይወት ትኖራለህና” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቀኖችህ እንዲረዝሙ

ረጅም ቀናት የረጅም ሕይወት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። እነዚህን ቃላት በዘዳግም 4፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። አ.ት፡ “ረጅም ጊዜ መኖር እንድትችል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 32:48

የአባሪም ተራሮች

ይህ ሞዓብ ውስጥ የሚገን የተራራ ሰንሰለት ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በናባው ተራራ አናት አባሪም

“አባሪም እና ናባው ተራራ ላይ ውጣ”

የናባው ተራራ

ይህ ከአባሪም ተራሮች ከፍተኛው ስፍራ ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በኢያሪኮ ትይዩ

“ከኢያሪኮ ከወንዙ በወዲያ ማዶ”

Deuteronomy 32:50

ወደ ሕዝብህ ተሰብሰብ

ይህ በሙታኑ ዓለም የሙሴ መንፈስ ከዘመዶቹ መንፈስ ጋር እንደሚገናኝ በትህትና የተነገረበት መንገድ ነው። አ.ት፡ “ከአንተ በፊት ከሞቱት አባቶችህ ጋር ተገናኝ” (See: Euphemism)

የሖር ተራራ

ይህ በኤዶም ዳርቻ የሚገኝ ተራራ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

መሪባ

ይህ በበረሃው ውስጥ ሙሴ እግዚአብሔርን ያልታዘዘበት ስፍራ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የጺን ምድረበዳ

ይህ በይሁዳ በስተደቡብ ዳርቻ የሚገኝ ምድረበዳ ስም ነው(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 33

1 የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ ከመሞቱ በፊት ለእስራኤላውያን የሰው ቃለ ቡራኬ ይህ ነው። 2 እንዲህም አለ፦ እግዚአብሔር ከሲና መጣ፤ በእነርሱም ላይ ከሴይር እንደ ማለዳ ፀሐይ ወጣ፤ ከፋራን ተራራ አበራላቸው፤ከአእላፋት ቅዱሳኑ ጋር መጣ፤ በስተቀኙ የሚነድ እሳት ነበር። 3 በእርግጥ ሕዝቡን የምትወድ አንተ ነህ፤ ቅዱሳኑ ሁሉ በእጅህ ውስጥ ናቸው። ከእግርህ ሥር ሁሉ ይስገዳሉ፤ ከአንተ ትእዛዝ ይቀበላሉ፤ 4 ይህ ሙሴ የሰጠን ሕግ የያዕቆብ ጉባኤ ርስት ነው። 5 የሕዝቡ አለቆች ከእስራኤል ነገዶች ጋር ሆነው፤ በአንድነት በተሰበሰቡ ጊዜ፤ እግዚአብሔር በይሹሩን ላይ ንጉሥ ነበር። ሮቤል በሕይወት ይኑር፤ አይሙት። 6 የወገኖቹ ቁጥርም ጥቂት ይሁን። 7 ስለይሁዳ የተነገረው ባትኮት ይህ ነው። ሙሴም እንዲህ አለ፦ እግዚአብሔር ሆይ፥ የይዳን ጩኸት ስማ፤ ወደ ወገኖቹም እንደገና አምጣው። ስለእርሱ ተዋጋለት፤ አቤቱ ከጠላቶቹ ጋር ሲዋጋ ረዳቱ ሁን! 8 ስለ ሌዊም ሙሴ እንዲህ አለ፦ ቱሚምህና ኡሪምህ ለምትወደው ሰው ይሁን፤ ማሳህ በተባለው ቦታ ፈተንኸው፤ በመሪባም ውሃ ከእርሱ ጋር ተከራከርህ። 9 ስለ አባቱና ስለ እናቱ ሲናገርም፤ ስለ እነርሱ ግድ የለኝም አለ። ወንድሞቹን አልለያቸውም፤ ልጆቹንም አላወቃቸውም። ስለቃልህ ከለላ አደረገ፤ ኪዳንህንም ጠበቀ። 10 ሥርዓትህን ለያዕቆብ፤ ሕግህንም ለእስራኤል ያስተምራል። ዕጣን በፊትህ፤ ያሚቃጠለውን መሥዋዕት ሁሉ በምሠዊያህ ላይ ያቀርባል። 11 እግዚአብሔር ሆይ፥ ኃይሉን ሁሉ ባርክለት፤ በእጁ ሥራ ደስ ይበልህ፤ በእርሱ ላይ የሚነሡበትን ሽንጣቸውን ቁረጠው፤ ጠላቶቹንም እንደገና እንዳይነሡ አድርገህ ምታቸው። 12 ሙሴ ስለ ብንያም እንዲህ አለ፦ የእግዚአብሔር ወዳጅ የሆነ በእርሱ ተጠብቆ በሰላም ይረፍ፤ ቀኑን ሙሉ ይጋርደዋልና፤ እግዚአብሔር የሚወደውን ሰው በትክሻዎቹ መካከል ያርፋል። 13 መሴ ስለ ዮሴፍ ደግሞ እንዲህ አለው፦ እግአብሔር ምድሩን ይባርክ፤ ውድ በሆኑ ሰማያዊ ነገሮች፥ ጠል ከላይ በማውረድ፤ ከታች በጥልቅ በተንጣለለው ነገሮች ይባርክ። 14 ከፀሐይ በተሠሩ ምርጥ ፍሬ፤ ጨረቃም በምትሰጠው እጅግ መልካም ነገር፤ 15 ከጥንት ተራሮች በተገኘ ምርጥ ስጦታ፤ በዘላለማዊ ኮረብቶች ፍሬያማነት ይባርክ። 16 ምድር በምታስገኘው ውድ ስጦታና በብዛት በቁጥቋጦም ውስጥ በነበረው በእርሱ መልካም ሞገስ። እነዚህ ሁሉ በረከቶች በወንድሞቹ መካከል ገዥ በሆነው፤ በዮሴፍ ራስ ላይ ይውረድ። 17 በግርማው እንደ በኩር ኮርማ ነው፤ ዘንዶቹም የጎሽ ቀንዶች ናቸው። በእነርሱም ሕዝቦችን በምድር ዳርቻ ላይ ያሉትን እንኳ ሳይቀር ይወጋል፤ እነርሱም የኤፍሬም አሥር ሺዎቹ ናቸው። 18 ስለ ዛብሎንም ሙሴ እንዲህ አለ፦ ዛብሎን ሆይ፥ ወደ ውጭ በመውጣትህ፤ አንተም ይሳኮር በድንኳኖችህ ውስጥ ደስ ይበልህ። 19 እነርሱም አሕዛብን ወደ ተራራው ይጠራሉ፤ በዚያም የጽድቅን መሥዋዕት ያቀርባሉ። እነርሱም ከባሕሮች በአሸዋ ውስጥ የተደበቀውን ሀብት ያወጡበታል። 20 ስለ ጋድም ሙሴ እንዲህ አለ፦ የጋድን ግዛት የሚያሰፋ የተባረከ ይሁን! ክንድንና ራስን በመገነጣጠል፤ ጋድ እንደ አንበሳ በዚያ ይኖራል። 21 ለአለቃን ድርሻ ሆኖ የተጠበቀለትን ለም የሆነውን መሬት ለራሱ መረጠ። ከሕዝብ አለቆች ጋር መጣ። በእስራኤል ላይ የወሰነውን የእግዚአብሔርን ሥርዓትንና ፍርዱን ፈጸመ። 22 ስለ ዳንም ሙሴ እንዲህ አለ፦ ዳን ከባሳን ዘሎ የሚወጣ፤ የአንበሳ ደቦል ነው። 23 ስለ ንፍታሌምም ሙሴ እንዲህ አለ፦ ንፍታሌም በእግዚአብሔር ሞገስ ረክቶአል፤ በበረከቱም ተሞልቶአል፤ ባሕሩንና የደቡብን ምድር ይወርሳል። 24 ስለ አሴርም ሙሴ እንዲህ አለ፦ አሴር ከሌሎች ልጆች ይልቅ የተባረከ ይሁን፤ በወንሞቹ ዘንድ ተወዳጅ ይሁን፤ እግሩንም በዘይት ውስጥ ያጥልቅ። 25 በዘመንህና ደህንነትህ ሁሉ የደጃፍህ መቀርቀሪያ ብረትና ናስ ይሁን፤ ኃይልህም በዘመንህ ሁሉ ይኖራል። 26 አንተን ለመርዳት በሰማያት ላይ በግርማው በደመናትም የሚገሠግሥ፤ እንደ ይሽሩን አምላክ ያለ ማንም የለም። 27 ዘላለማዊ አምላክ መኖርያህ ነው፤ የዘላለም ክንዶቹም ከበታችህ ናቸው፤ እርሱን አጥፋው! በማለት፤ ጠላትህን ከፊትህ ያስወግደዋል። 28 ስለዚህ እስራኤል በሰላም ይሆራል።። የሰማያት ጠል በሚወርድበት፤ እህልና የወይን ጠጅ ባለበት ምድር የያዕቆብን ምንጭ የሚነካው የለም። 29 እስራኤል ሆይ፥ አንተ ቡሩክ ነህ፤ እግዚአብሔር ያዳነው ሕዝብ፤ እንዳንተ ያለ ማን ነው? እርሱ ጋሻህና ረዳትህ፤ የክብርህም ሰይፍ ነው። ጠላቶችህ ተሸብራው በፍርሃት፤ ወደ አንተ ይመጣሉ። አንተም ከፍታቸውን መረማመጃ ታደርጋለህ።



Deuteronomy 33:1

እግዚአብሔር ከሲና መጣ፣ ከሴይርም በእነርሱ ላይ ተነሣ። ከፋራን ተራራ አበራ

ሙሴ እግዚአብሔርን ከንጋት ፀሐይ ጋር ያነጻጽራል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ከሲና በመጣ ጊዜ ከሴይር ወጥታ ከፋራን ተራራ የምታበራዋን ፀሐይ መስሎ ታይቷቸው ነበር” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእነርሱ ላይ

“በእስራኤል ሕዝብ ላይ”

አሥር ሺህ ቅዱሳኑ

“10000 መላእክት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በቀኝ እጁ የሚያበራ መብረቅ ነበር

ሊሆኑ የሚችሉ ሌሎች ትርጉሞች 1) “በቀኝ እጁ የእሳት ነበልባል ነበር” ወይም 2) “የእሳትን ሕግ ሰጣቸው” ወይም 3) “ተራሮቹን ቁልቁል በመውረድ ከደቡብ መጣ”

Deuteronomy 33:3

ሕዝቡ

“የእስራኤል ሕዝብ”

ቅዱሳኑ ሁሉ በእጅህ ውስጥ ናቸው == እግርህ -- ቃሎችህ

የተጸውዖ ስሞች የሆኑት “የእርሱ” እና “የአንተ” የሚያመለክቱት እግዚአብሔርን ነው። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር ቅዱሳን ሁሉ በእጁ ውስጥ ናቸው . . . እግሩ . . . ቃሎቹ” (ተውላጠ ስም የሚለውን ተመልከት)

ቅዱሳኑ ሁሉ በእጅህ ውስጥ ናቸው

እጅ የኃይል እና የጥበቃ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ቅዱስ ሕዝቡን ሁሉ አንተ ትጠብቃለህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ርስት

“ንብረት” ወይም “ዋጋው ውድ የሆነ ንብረት”

Deuteronomy 33:5

ንጉሥ ነበር

“እግዚአብሔር ነገሠ”

ይሹሩን

ይህ የእስራኤል ሌላው ስሙ ነው። ይህንን በዘዳግም 32፡15 እንዳለው አድርገህ ተርጉመው።

ሮቤል በሕይወት ይኑር

ሙሴ እያንዳንዱን የእስራኤል ነገዶች መባረኩን በዚህ ይጀምራል።

ሆኖም የእርሱ ሰዎት ጥቂቶች ይሁኑ

ሊሆኑ የሚችሉ ሌሎች ትርጉሞች 1) “የእርሱ ሰዎች ጥቂቶች አይሁኑ” ወይም 2) “የእርሱ ሰዎች ጥቂቶች ቢሆኑም እንኳን”

Deuteronomy 33:7

ለይሁዳ ድምፅ

እዚህ ጋ “የይሁዳ ድምፅ” የይሁዳን ሕዝብ ጩኸትና ጸሎት ያመለክታል። አ.ት፡ “የይሁዳ ሕዝብ ወደ አንተ በጸለየ ጊዜ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ረዳቱ ሁን

የነገር ስም የሆነው “ረዳት” እንደ ግሥ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እንዲዋጋ እርዳው” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 33:8

ቱሚምህና ኡሪምህ

እነዚህ ሊቀ ካህናቱ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ በሚፈልግበት ጊዜ በደረቱ ላይ የሚሸከማቸው ቅዱስ ድንጋዮች ነበሩ። እዚህ ጋ “የአንተ” የሚያመለክቱት እግዚአብሔርን ነው። (See: Forms of You እና የማይታወቁትን ተርጉማቸው የሚለውን ተመልከት)

ለአንተ ታማኝ የሆነ

“ለአንተ ቅዱስ የሆነ” ወይም “አንተን ደስ ለማሰኘት የሚፈልገው”። ይህ የሌዊን ነገድ ያመለክታል።

ማሳህ

ይህንን በዘዳግም 6፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። ተርጓሚው፣ “ ‘ማሳህ’ ማለት ‘መፈተን’ ማለት ነው” የሚል የግርጌ ማስታወሻ መጨመር ይችላል።

መሪባ

ይህንን በዘዳግም 32፡51 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። ተርጓሚው፣ “ ‘መሪባ’ ማለት ‘መከራከር’ ወይም ‘መጣላት’ ማለት ነው” የሚል የግርጌ ማስታወሻ መጨመር ይችላል።

Deuteronomy 33:10

የአንተ == የአንተ == አንተ == የአንተ

ሙሴ ለእግዚአብሔር እየተናገረ ነው፣ ስለዚህ እነዚህ ቃላት ሁሉ ነጠላ ቁጥሮች ናቸው።

Deuteronomy 33:11

ተቀበል

በእርሱ ደስ ይበልህ

የእጆቹን ሥራ

እዚህ ጋ “እጆች” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሙሉውን ሰው ነው። አ.ት፡ “እርሱ የሠራውን ሥራ ሁሉ” (See: Synecdoche)

ወገባቸውን ሰባብር

ወገብ የጉልበት ማዕከል እንደሆነ ይታሰባል፣ እዚህ ጋ የሚወክለውም ጉልበትን ነው። አ.ት፡ “ጉልበታቸውን ውሰድ” ወይም “ፈጽመህ አጥፋ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ተነሥ == ተነሥ

ይህ ሐረግ ዘይቤአዊ አነጋገር ሆኖ ሁለት ጊዜ ጥቅም ላይ ውሏል። አ.ት፡ “ለመዋጋት ተነሥ . . . እንዳያንሠራሩ አድርጋቸው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በ -- ላይ ተነሥ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ከ -- ጋር ተዋጋ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 33:12

በእግዚአብሔር የተወደደ -- ይኖራል

እዚህ ጋ ሙሴ የሚያመለክተው የብንያም ነገድ አባላትን ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በሕይወት እንዲኖሩ የሚወድላቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በደኅንነት ይኖራል

የነገር ስም የሆነው “ደኅንነት” ግሣዊ ሐረግ በመጠቀም ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ማንም ሊጎዳው በማይችልበት ስፍራ ይኖራል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

በእግዚአብሔር ክንዶች መካከል ይኖራል

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) እግዚአብሔር የብንያምን ነገድ በኃይሉ ይከላከልላቸዋል ወይም 2) እግዚአብሔር በብንያም ነገድ ኮረብታማ አካባቢ ይኖራል። በሁለቱም ትርጉሞች፣ እግዚአብሔር ይንከባከባቸዋል የሚል አንድምታ አለው።

Deuteronomy 33:13

ስለ ዮሴፍ

ይህ የሚያመለክተው የኤፍሬምንና የምናሴን ነገዶች ነው። ሁለቱም ነገዶች የተገኙት ከዮሴፍ ነው።

የእርሱ ምድር በእግዚአብሔር ይባረክ

“የእርሱ” የሚለው ቃል የኤፍሬምንና የምናሴን ነገዶች የሚወክለውን ዮሴፍን ያመለክታል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ምድራቸውን ይባርክ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከሰማይ በሆኑ የከበሩ ነገሮች፣ በጠል

“ከሰማይ በሆነ የከበረ ጠል” ወይም “ከሰማይ በሆነ የከበረ ዝናብ”

ጠል

ቅዝቃዜ ባለው ማለዳ ላይ በቅጠልና ሣር ላይ ውሃ የሚፈጥር። ይህንን በዘዳግም 32፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ከታች በሚተኛ ጥልቅ

ይህ በከርሠ ምድር ውስጥ የሚገኘውን ውሃ ያመለክታል።

Deuteronomy 33:14

የእርሱ ምድር ይባረክ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 33፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ምድሩን ይባርክ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከፀሐይ በሚሆን የከበሩ ነገሮች መከር

“ፀሐይ እንዲበቅሉ በሚያደርጋቸው ምርጥ ሰብሎች”

ወራት በሚያስገኙት የከበሩ ነገሮች

“ከወር እስከ ወር በሚበቅሉ ምርጥ ሰብሎች”

ምርጥ ነገሮች -- የከበሩ ነገሮች

ሙሴ ምናልባት የምግብ ሰብሎችን ሳያመለክት አይቀርም። የዚህ አነጋገር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እጅግ ምርጥ የሆኑ ፍሬዎች . . . የከበሩ ፍሬዎች” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

የጥንት ተራሮች

“ከረጅም ዘመን ጀምሮ የኖሩ ተራሮች”

የዘላለም ኮረብቶች

“ለዘላለም የሚኖሩ ኮረብቶች”

Deuteronomy 33:16

የእርሱ ምድር ይባረክ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። ይህንን በዘዳግም 33፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “የእርሱን ምድር እግዚአብሔር ይባርክ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ብዛቱን

x

Deuteronomy 33:17

በግርማው እንደ በኩር በሬ ነው

በሬ በዘይቤአዊ አነጋገር ትልቅና ጉልበታም የሆነን ነገር ያመለክታል። “በኩር” የሚለው ቃል በዘይቤአዊ አነጋገር ክብር ማለት ነው። አ.ት፡ “ሰዎች ብዙና ኃያላን የሆኑትን የዮሴፍን ተወላጆች ያከብሯቸዋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቀንዶቹ የ -- ቀንዶች ናቸው

ቀንድ የብርታት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “እርሱ እንደ -- ብርቱ ነው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእነርሱ ይገፋል

በቀንዶቹ መግፋቱ ስለ ብርታቱ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “እርሱ በጣም ብርቱ ስለሆነ ይገፋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የኤፍሬም አሥር ሺዎች -- የምናሴ ሺዎች

ይህ ማለት የኤፍሬም ነገድ ከምናሴ ነገድ ይልቅ ይበረታል። አ.ት፡ “የኤፍሬም ሕዝብ ከ10000 ብዙ ዕጥፍ . . . (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 33:18

ዛብሎን በመውጣትህ፣ አንተም ይሳኮር በድንኳኖችህ ደስ ይበልህ

የዛብሎን ሕዝብ የሚገኙት በሜዴትራንያን ባህር አጠገብ ነበር። በባህር ላይ እየተጓዙ ከሌሎች ሕዝቦች ጋር ይገበያዩ ነበር። የይሳኮር ሕዝቦች በእርሻና ከብት በማርባት ሰላማዊ ኑሮን የሚመርጡ ነበሩ። በውስጠ ታዋቂነት ያሉ መረጃዎችን ግልጽ ልታደርጋቸው ትችላለህ። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

እነርሱ በዚያ ያቀርባሉ

“እነርሱ የሚያቀርቡት በዚያ ነው”

የጽድቅን መሥዋዕት

“ተቀባይነት ያላቸውን መሥዋዕቶች” ወይም “ተገቢነት ያላቸውን መሥዋዕቶች”

ከባህር የሚትረፈረፈውን ይጠባሉና፣ በባህር ዳር ካለው አሸዋም የሚገኘውን

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) በባህሩ ማዶ ካሉ ሕዝቦች ጋር ይገበያያሉ ወይም 2) አሸዋን በመጠቀም የሸክላ ሥራ መሥራት ጀምረው ነበር።

ከባህር የሚትረፈረፈውን ይጠባሉና

እዚህ ጋ “መጥባት” የሚለውን ቃል የዕብራይስጡ ትርጉም አንድ ሕፃን ልጅ የእናቱን ጡት እንዴት እንደሚመገብ ያመለክታል። ይህ ማለት አንድ ሕፃን ከእናቱ ወተት እንደሚያገኝ ሕዝቡ ከባህር ሀብት ያገኛሉ። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Deuteronomy 33:20

ጋድን የሚያሰፋው የተባረከ ይሁን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) “እግዚአብሔር ጋድን ይባርከው፣ የሚኖርበትንም ብዙ መሬት ይስጠው” ወይም 2) ለጋድ የሚኖርበትን ብዙ ምድር ሰጥቶታልና ሰዎች እግዚአብሔር መልካም ነው ይበሉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እንደ ሴት አንበሳ በዚያ ይኖራል፣ ክንድንና ራስንም ይገነጣጥላል

ይህ ማለት የጋድ ሕዝብ ብርቱና ደህንነቱ የተጠበቀ ስለሆነ በጦርነት ጠላቶቻቸውን ያሸንፋሉ። (See: Simile)

Deuteronomy 33:22

ዳን ከባሳን ዘሎ የሚወጣ የአንበሳ ደቦል ነው

የዳን ሕዝብ እንደ አንበሳ ደቦል ብርቱዎች ናቸው፣ በባሳን የሚኖሩትን ጠላቶቻቸውን ወጉ። በውስጠ ታዋቂነት ያሉትን መረጃዎች ግልጽ ልታደርጋቸው ትችላለህ። (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር እና Ellipsis የሚለውን ተመልከት))

Deuteronomy 33:23

ዳን ከባሳን ዘሎ የሚወጣ የአንበሳ ደቦል ነው

የዳን ሕዝብ እንደ አንበሳ ደቦል ብርቱዎች ናቸው፣ በባሳን የሚኖሩትን ጠላቶቻቸውን ወጉ። በውስጠ ታዋቂነት ያሉትን መረጃዎች ግልጽ ልታደርጋቸው ትችላለህ። (See: (ዘይቤአዊ አነጋገር እና Ellipsis የሚለውን ተመልከት))

በሞገስ ረክቷል

እግዚአብሔር በንፍታሌም መደሰቱ “ሞገስ” ምግብ ሆኖ ንፍታሌም ዳግመኛ እስከማይራብ ድረስ የበላው በሚመስል መልኩ ተነግሮለታል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በእርሱ ስለ ተደሰተበት የሚፈልገው መልካም ነገሮች ሁሉ አሉት” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የእግዚአብሔር በረከት ሙላት

በረከቶች ምግብ ሆነው ንፍታሌም ተጨማሪ መያዝ እስከማይችል ድረስ የበላው በሚመስል መልኩ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ስለ ባረከው የሚፈልገው ሁሉ አለው”

ሀብት ውሰድ

ሙሴ የንፍታሌምን ነገድ አንድ ሰው እንደ ሆኑ አድርጎ ይናገራል፣ ስለዚህ እነዚህ ቃላት ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

በስተምዕራብና በስተደቡብ ያለ ምድር

ይህ በገሊላ ሐይቅ ዙሪያ ያለውን ምድር ያመለክታል። የዚህ ንግግር ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 33:24

እግሩን በወይራ ዘይት ውስጥ ያጠልቃል

የወይራ ዘይት ለምግብነትና ለፊትና ለክንድ ቆዳ ጥቅም ላይ ይውል ነበር። እግር ይቆሽሻል፣ ስለዚህ እግርን በወይራ ዘይት ውስጥ መጨመር ዋጋ ያለውን ዘይት ማበላሸት ይሆናል። የዚህ ንግግር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ማባከን እንዲቻለው ብዙ የወይራ ዘይት ይኑረው” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

የከተማህ የበር መቀርቀሪያዎች - ቀኖችህ - ደህንነትህ

አንድ ሰው የሆኑ ይመስል ሙሴ የሚናገረው ለአሴር ነገድ ነው፣ ስለዚህ “የአንተ” የሚሉት አገባቦች ሁሉ ነጠላ ቁጥሮች ናቸው። (See: Forms of You)

የከተማህ በር መቀርቀሪያዎች ብረትና ነሐስ ይሁኑ

ከተሞች ጠላት እንዳይገባባቸው በበሮቻቸው አግድመት ላይ ረጃጅም መቀርቀሪያዎች ይኖራቸው ነበር። የዚህ ንግግር ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በጠላቶችህ ከመጠቃት እንድትድን” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 33:26

ይሹሩን

ይህ የእስራኤል ሕዝብ ሌላው ስሙ ነው። ትርጉሙም “ቀጥተኛ የሆነ” የሚል ነው። ይህንን በዘዳግም 32፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።(ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በሰማያት መካከል የሚራመድ -- በደመና ላይ

በጦር ሜዳ ላይ በሠረገላው እንደሚሄድ ንጉሥ በጠፈር መካከል በደመና ላይ የሚሄድ ይህ የእግዚአብሔር ምስል ነው። አ.ት፡ “ንጉሥ በጦር ሜዳ መካከል እንደሚሄድ በሰማያት መካከል ይሄዳል. . . በሠረገላው እንዳለ ንጉሥ በደመናት ላይ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሊረዳህ

“አንተን ለመርዳት” ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚለው ቃል እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

Deuteronomy 33:27

የዘላለም አምላክ መጠጊያ ነው

የነገር ስም የሆነው “መጠጊያ” መጠለያ ወይም ከአደጋ ማምለጫ ስፍራ ማለት ሲሆን እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የዘላለም አምላክ ሕዝቡን ይጠብቃል” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

የዘላለም ክንዶች ከበታች ናቸው

“የዘላለም ክንዶች” የሚሉት ቃላት እግዚአብሔር ሕዝቡን ለዘላለም እንደሚጠብቃቸው ለሰጠው ተስፋ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ሕዝቡን ለዘላለም ይረዳቸዋል፣ ይንከባከባቸዋልም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

-በማለት ወግቶ ያስወጣቸዋል

ሙሴ እርሱ የሚናገረው የሚፈጸም ስለመሆኑ አጽንዖት ለመስጠት ወደፊት ሊሆን ያለውን ባለፈ ጊዜ እንደሆነ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “እርሱ ወግቶ ያስወጣቸዋል. . . ይላል” (See: Predictive Past)

በፊትህ -- አጥፋው

ሙሴ እስራኤላውያንን እንደ አንድ ሰው አድርጎ ይናገራቸዋል፣ ስለዚህ “አንተ” የሚለው ቃልና “አጥፋው” የሚለው ትዕዛዝ እዚህ ጋ ነጠላ ቁጥር ነው። (See: Forms of You)

“አጥፋው!” ይላል

በአንተ ቋንቋ ይህ ቀጥተኛ ትዕምርተ ጥቅስ በሚገባ የማያገለግል ከሆነ ቀጥተኛ ወዳልሆነው ትዕምርተ ጥቅስ ልትለውጠው ትችላለህ። አ.ት፡ “እንድታጠፋቸው ይነግርሃል” (See: Direct and Indirect Quotations)

Deuteronomy 33:28

እስራኤል ይኖራል -- የያዕቆብ ምንጭ የተጠበቀ ነበር

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ሙሴ እርሱ የሚናገረው የሚፈጸም ስለመሆኑ አጽንዖት ለመስጠት ወደፊት ሊሆን ያለውን ባለፈ ጊዜ እንደሆነ አድርጎ ይናገራል። “እስራኤል ይኖራል . . . የያዕቆብ ምንጭ የተጠበቀ ይሆናል” ወይም 2) ሙሴ፣ “እስራኤል ይኑር . . . የያዕቆብ ምንጭም የተጠበቀ ይሁን” በማለት እስራኤልን እየባረከ ነው የሚሉት ናቸው። (See: Predictive Past)

የያዕቆብ ምንጭ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) የያዕቆብ ቤት ወይም 2) የያዕቆብ ተወላጆች (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰማያቱ ጠልን ያንጠባጥቡ

ጠል የዝናብን ያህል አስፈላጊ ስለመሆኑ ተነግሯል። ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ሙሴ “እንደ ዝናብ ብዙ ጠል ምድሪቱን ይሸፍናት” በማለት እስራኤልን እየባረከ ነው ወይም 2) ሙሴ “ብዙ ጠል እንደ ዝናብ ምድሪቱን ይሸፍናታል” በማለት ወደ ፊት ምን ሊሆን እንዳለ ይነግራቸዋል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ጠል

ቅዝቃዜ ባለበት ጠዋት በቅጠሎችና በሣር ላይ የሚገኝ ውሃ። ይህንን በዘዳግም 32፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Deuteronomy 33:29

በግርማ -- እንዳንተ ያለ፣ በእግዚአብሔር የዳነ ሕዝብ ማነው?

ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እንደ ንግግር ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። ድግሞም በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እንደ አንተ ያለ እግዚአብሔር ያዳነው የሕዝብ ወገን የለም . . . በግርማ”። (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ጋሻ -- ሰይፍ

ይህ አገላለጽ እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከጠላቶቻቸው እንደሚከላከልላቸውና ጠላቶቻቸውን እንዲወጉ እንደሚያስችላቸው ይናገራል። (See: Merism)

የረዳትህ ጋሻ

“ጋሻ” የሚለው ቃል እግዚአብሔር እስራኤላውያንን የመጠበቁና የመከላከሉ ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። የነገር ስም የሆነው “ረዳት” እንደ ግሥ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “አንተን የሚጠብቅህና የሚረዳህ” (ዘይቤአዊ አነጋገር እና የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

የግርማዊነትህ ስይፍ

“ሰይፍ” የሚለው ቃል ጦርነቶችን ለማሸነፍ በሰይፍ ለመግደል ኃይል ማግኘትን የሚያመለክት ዘይቤአዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ግርማ እንዲኖርህና ጦርነቶችን እንድታሸንፍ የሚያስችልህ እርሱን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የከፍታ ስፍራቸውን ትረግጣለህ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ሌሎች ሕዝቦች ሐሰተኞች አማልክትን ያመለኩባቸውን ስፍራዎች እስራኤላውያን ይደመስሱታል ወይም 2) እስራኤላውያን ጠላቶቻቸውን ድል በሚያደርጉበት ጊዜ በጀርባቸው ላይ ይረማመዱባቸዋል።


Chapter 34

1 ሙሴ ከሞዓብ ሜዳ ተነሥቶ ለኢያሪኮ ትይዩ ወደ ሆነው ፈስጋ ጫፍ ወደ ናባው ተራራ ሄደ። በዚያም እግዚአብሔር ከገለዓድ እስከ ዳን ያለውን ምድሪቱን ሁሉ፤ 2 ንፍታሌምን ሁሉ፥የኤፍሬምንና የምናሴን ግዛት እስከ ምዕራብ ባሕር ድረስ ያለውን የይሁዳን ምድር ሁሉ አሳየው፤ 3 ኔጌብንና የዘንባባ ከተማ ከሆነችው ከኢያሪኮ ሸለቆ እስከ ዞዓር ያለውን ምድር ሁሉ አሳየው። 4 ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር ለአብርሃም፥ ለይስሐንና ለያዕቆብ ለአባቶቻችሁ እሰጣለሁ ብዬ በመሐላ ቃል የገባሁላቸው ምድር፥ በዐይንህ እንድታያት አድርጌአለሁ፤ ነገር ግን ወደዚያ አትሻገርም አለው። 5 እግዚአብሔር እንደተናገረው የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ በሞዓብ ምድር ሞተ። 6 በሞዓብ ምድር በቤተ ፌጎር ፊት ለፊት ባለው ሸለቆ እግዚአብሔር ቀበረው፤ ይሁን እንጂ መቃብሩ የት እንደ ሆን እስከ ዛሬ ማንም አያውቅም። 7 ሙሴ በሞተ ጊዜ ዕድሜው መቶ ሃያ ዓመት ነበር፤ ሆኖም ዐይኑ አልፈዘዘም፤ ጉልበቱም አልደከመም። 8 የልቅሶውና የሐዘኑ ጊዜ እስኪያበቃ ድረስ እስራኤላውያን በሞዓብ ሜዳ ሠላሳ ቀን አለቀሱለት። 9 ሙሴ እጆቹን ጭኖበት ስለ ነበር የነዌ ልጅ ኢያሱ በጥበብ መንፈስ ተሞላ። ስለዚህ እስራኤላውያን ሁሉ አደመጡት፤ እግዚአብሔር ሙሴን አዞት የነበረውንም ሁሉ አደረገ። 10 እግዚብብሔር ፊት ለፊት ያወቀው እንደ ሙሴ ያለ ነቢይ ከዚያ ወዲህ በእስራኤል አልተነሣም። 11 እግዚአብሔር ልኮት እነዚያን ታምራዊ ምልክቶችና ድንቆች ሁሉ በግብፅ በፈርዖን በሹማምንቱና በምድሪቱ ሁሉ ላይ እንዲያደርግ የላከውን ያደረገ ማንም ሰው አልነበረም። 12 ሙሴ በእስራኤል ሁሉ ፊት ያሳየውን ታላቅ ኃይል ያሳየ ወይም ያደረገውን አስደናቂ ተግባር የፈጸመ ማንም ነቢይ የለም።



Deuteronomy 34:1

የናባው ተራራ

ይህ ከአባሪም የተራራ ሰንሰለት በስተሰሜን የሚገኝ የፈስጋ ተራራ ጫፉ ነው። ይህንን በዘዳግም 32፡49 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ፈስጋ

ይህንን በዘዳግም 3፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የዘንባባ ከተማ

x

Deuteronomy 34:4

ቤተ ፌጎር

ይህ በሞዓብ የነበረ መንደር ነው። ይህንን በዘዳግም 3፡29 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

በዐይኖችህ ተመልከተው

“ለራስህ ተመልከተው”

እስከ ዛሬ ድረስ

ይህ የሚያመለክተው ይህ የተጻፈበትን ወይም የታረመበትን ጊዜ እንጂ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ውስጥ ያለውን የአሁኑን ጊዜ አይደለም።

Deuteronomy 34:7

የአንድ መቶ ሃያ ዓመት ዕድሜ -- ሠላሳ ቀን

“የ120 ዓመት ዕድሜ . . . 30 ቀን” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ዐይኑ አልፈዘዘም፣ የተፈጥሮ ጉልበቱም አልደከመም

ይህ ማለት ዐይኖቹና አካሉ ገና ብርቱና ጤናማ ነበሩ ማለት ነው።

Deuteronomy 34:9

የነዌ ልጅ

ይህንን በዘዳግም 1፡38 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ኢያሱ -- በጥበብ መንፈስ ተሞልቶ ነበር

ጸሐፊው ኢያሱን አንድን ነገር እንደሚይዝ ዕቃ፣ መንፈስን ደግሞ በመያዣው ውስጥ እንደሚጨመር ቁሳዊ አካል አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “ . . . በጣም ጥበበኛ እንዲሆን እግዚአብሔር ኢያሱን አስቻለው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሙሴ እጆቹን በእርሱ ላይ ጭኖበት ነበር

የዚህ ንግግር ሙሉ ትርጉም ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ኢያሱ እግዚአብሔርን እንዲያገለግል ለመለየት ሙሴ እጆቹን በእርሱ ላይ ጭኖበት ነበር” (See: Assumed Knowledge and Implicit Information)

Deuteronomy 34:10

እግዚአብሔር ፊት ለፊት ያወቀው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ይህ ማለት እግዚአብሔርና ሙሴ በጣም የቀረበ ግንኙነት ነበራችው ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በታላላቆቹ ሁሉ

“ታላላቆቹን ሁሉ ያደረገ”


Book: Joshua


Joshua

Chapter 1

1 እንዲህም ሆነ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ ከሞተ በኋላ እግዚአብሔር የሙሴ ዋና ረዳት የሆነውን የነዌ ልጅ ኢያሱን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 2 አገልጋዬ ሙሴ ሞቶአል። ስለዚህም ለእስራኤል ልጆች ወደምሰጣቸው ምድር አንተና ይህ ሕዝብ ሁሉ ተነሥታችሁ ይህን ዮርዳኖስ ተሻገሩ። 3 የእግራችሁ ጫማ የሚረግጥውን ቦታ ሁሉ ለእናንተ ሰጥቼአለሁ።ለሙሴም ተስፋ እንደ ሰጠሁት ሰጥቻችኋለሁ። 4 ከምድረ በዳው ከዚህም ከሊባኖስ ጀምሮ እስከ ታላቁ ወንዝ እስከ ኤፍራጥስ ድረስ፤ የኪጢያውያን ምድር ሁሉ እስከ ፀሐይ መግቢያ እስከ ታላቁ ባሕር ድረስ ዳርቻእሁ ይሆናል። 5 በሕይወትህ ዘመን ሁሉ ማንም ሊቋቋምህ አይችልም። ከሙሴ ጋር እንደ ነበርሁ እንዲሁ ከአንተ ጋር እሆናለሁ። አልጥልህም አልትውህም። 6 ለአባቶቻቸው፦እሰጣችኋለሁ ብዬ ተስፋ የሰጠ'ኋችሁውን ምድር ይህ ሕዝብ እንዲወርስ ታደርጋለህና ጽና አይዞህ። 7 ስለዚህም ጽና እጅግ በርታ። አገልጋዬ ሙሴ ያዘዘህን ሕግን ሁሉ ትጠብቀው ዘንድ ተጠንቀቅ። በምትሄድበትም ሁሉ እንዲከናወንልህ ወደ ቀኝ ወይም ወደ ግራ አትበል። 8 ስለዚህ ሕግ መጽሐፍ ሁልጊዜ ተናገር። የተጻፈበትንም ሁሉ ትጠብቅ ዘንድ በቀንና በሌሊትም አሰላስለው። የዚያን ጊዜም የተከናወነልህና የተሳከልህ ትሆናለህ። 9 በምትሄድበት ሁሉ አምላክህ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነውና፦ "ጽና፥ አይዞህ፥ አትፍራ፥ ተስፋ አትቁረጥ ብዬ አላዘዝሁህምን?" 10 ኢያሱም የሕዝቡን አለቆች እንዲህ ብሎ አዘዘ፦ 11 "በሰፈሩ መካከል እለፉ፤ ሕዝቡንም፦ ለራሳችሁ ስንቃችሁን አዘጋጁ ብላችሁ እዘዙአቸው። እግዚአብሔር አምላካችሁ እንዲትወርሱ ወደሚሰጣችሁ ምድር በሦስት ቀናት ውስጥ ይህን ዮርዳኖስን ተሻግራችሁ ትወርሳላችሁ። 12 ኢያሱም የሮቤልን ልጆች የጋድንም ልጆች የምናሴንም ነገድ እኩሌታ እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፦ 13 የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ እንዲህ ብሎ ያዘዛቸውን ቃል አስቡ፦አምላካችሁ እግዚአብሔር እረፍት ይሰጣችኋል፤ይህንንም ምድር ይሰጣችኋል። 14 ሚስቶቻችሁ፥ ልጆቻችሁና ከብቶቻችሁ ሙሴ በዮርዳኖስ ማዶ በሰጣችሁ ምድር ይቀመጣሉ። ነገር ግን ተዋጊ የሆኑ ሰዎቻችሁ እግዚአብሔር ለእናንተ እንደሰጣችሁ 15 ወንድሞቻችሁን እረፍት እስኪሰጥ ድረስ ከወንድሞቻችሁ ፊት በመሆን እነርሱንም ለመርዳት ይሄዳሉ ። እነርሱም ደግሞ አምላካችሁ እግዚአብሔር የሚሰጣቸውን ምድር ይወርሳሉ። ከዚያም በኋላ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ ብዮርዳኖሴ ማዶ በፀሐይ መውጫ ወደሰጣችሁ ወደ ርስታችሁ ትመለሳላችሁ፤ ትወርሳላችሁም። 16 እነርሱም ለኢያሱ እንዲህ ብለው መለሰለት፦ያዘዝኸንን ነገር ሁሉ እናደርጋለን፤ ወደምትልከንም ስፍራ ሁሉ እንሄዳለን። 17 ለሙሴ እንደ ታዘዝን ለአንተ ደግሞ እንታዘዛለን። ከሙሴ ጋር እንደ ነበረ እግዚአብሔር አምላክህ ብቻ ከአንተጋር ይሁን። 18 በትእዛዝህ ላይ የሚያምፅና ቃልህን የማይታዘዝ ማንም ቢሆን ይገደል። ብቻ ጽና፥ በርታ።



Joshua 1:1

ያህዌ

ይህ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለህዝቡ ራሱን የገለጸበት ስም ነው፡፡ ይህንን እንዴት እንደሚተረጉሙት ስለ ያህዌ የቃል ትርጉም ገጽ/ጽሁፍን ይመልከቱ፡፡

ነዌ

የኢያሱ አባት (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህንን ዮርዳኖስን አቋርጡ

"ማቋረጥ" ማለት "ከወንዙ ማዶ መሄድ/ወንዙን ማቋረጥ" ማለት ነው፡፡ "ከዚህ ዳርቻ ወደ ዮርዳኖስ ወዲያኛው ዳርቻ መሄድ/ማቋረጥ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አንተ እና ይህ ህዝብ ሁሉ

"አንተ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ኢያሱን ነው፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮች ይመልከቱ)

ሁሉንም ስፍራ ሰጥቼሃለሁ

እግዚአብሔር ምድሪቱን በመጭው ጊዜ ለእስራኤል መስጠቱ የተገለጸው አስቀድሞ እንደሰጣቸው ተደርጎ ነው፡፡ ይህ ምድሪቱን በእርግጥ እንደሚሰጣቸው አጉልቶ ያሳያል፡፡ "ለእናንተ ሁሉንም ስፍራ እሰጣችኋለሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (የወደፊት ሃላፊ ጊዜ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእናንተ ሰጥቻለሁ

"እናንተ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ኢያሱን እና የእስራኤል ህዝብን ሁለቱንም ነው፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮችን ይመልከቱ)

የእግራችሁ ጫማ የሚረግጠውን ስፍራ ሁሉ

ይህ የሚያመለክተው የዮርዳኖስን ወንዝ ሲያቋርጡ ኢያሱ እና እስራኤላውያን የሚጎዙበትን ስፍራ ሁሉ ነው፡፡ "በዚህ ምድር በምትሄዱበት ሁሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 1:4

አጠቃላይ መረጃ ፡

ያህዌ ከኢያሱ ጋር ንግግሩን ቀጠለ

የአንተ ምድር

"የአንተ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ኢያሱን ብቻ ሳይሆን የእስራኤልን ነገዶች በሙሉ ነው፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮችን ይመልከቱ)

በፊትህ ለመቆም

በቁጥር 5 "አንተ" እና "የአንተ" የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት ኢያሱን ነው፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮችን ይመልከቱ)

እኔ አንተን አልተውህም ወይም አልጥልህም

"መተው" እና "መጣል" የሚሉት ቃላት በመሰረታዊነት አንድ አይነት ነገሮች ናቸው፡፡ ያህዌ እነዚህን አንድ ላይ ያጣመራቸው እዘኒህን ነገሮች እንደማያደርግ ለማጉላት ነው፡፡ "በእርግጥ ሁልጊዜም ከአንተ ጋር እሆናለሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ጥንድ ትርጉም እና ጥንድ አሉታዎች የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 1:6

አጠቃላይ መረጃ ፡

ያህዌ ለኢያሱ ጥብቅ ትዕዛዛትን ሰጠው (ሃላፊነቶች -ሌሎች ጥቅሞች የሚለውን ይመልከቱ)

በርታ ደግሞም ጽና

ያህዌ ኢያሱን በጽናት ፍርሃቶቹን እንዲያሸንፍ ያዘዋል፡፡ (ሃላፊነቶች -ሌሎች ጥቅሞች የሚለውን ይመልከቱ)

ከዚህ ወደ ቀኝ ወይም ወደ ግራ አትበል

ይህ በአዎንታዊ ትዕዛዝ ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ይህንን በትክክል ተከተል" ወይም "በትክክል ተከተላቸው" (ሃላፊነቶች -ሌሎች ጥቅሞች የሚለውን ይመልከቱ)

ፍሬያማ ሁን

"ግብህን ጨብጥ" ወይም "ግብህ ላይ ድረስ"

Joshua 1:8

አጠቃላይ መረጃ ፣

ያህዌ ከኢያሱ ጋር ንግግሩን ቀጠለ

ሁልጊዜም ትናገራለህ

"ሁልጊዜ" የሚለው ቃል ብዙ ጊዜ መናገር ተጋኖ የተገለጸበት ነው፡፡ (ኩሸት እና ማጠቃለል የሚሉትን ይመልከቱ)

የበለጸገ እና ስኬታማ

አነዚህ ሁለት ቃላት በመሰረቱ አንድ ትረጉም ይዘዋል እናም ታላቅ ብልጽግናን ያጎላሉ፡፡ (ጥንድ ትርጉም የሚለውን ይመልከቱ)

እኔ አላዘዝኩህምን?

ይህ ያህዌ ኢያሱን ማዘዙን ያመለክታል፡፡ "እኔ አዝዤሃለሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

በርታ ደግሞም ጽና!

ያህዌ ኢያሱን እያዘዘው ነው፡፡ (ሃላፊነቶች -ሌሎች ጥቅሞች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 1:10

ወደ ሰፈር ገብታችሁ ‘ተዘጋጁ… ውረሱ' ብላችሁ ህዝቡን እዘዙ፡፡'

በጥቅስ ውስጥ ቀረበው ቀጥተኛ ባለሆነ ጥቅስ ሊገለጽ ይችላል፡፡ "ወደ ሰፈር ግቡ ህዝቡ ለራሱ የሚሆነውን እንዲያዘጋጅ እዘዙ፡፡ በሶስት ቀናት ውስጥ ይህንን ዮርዳኖስን አቋርጠው ያህዌ አምላካቸው እንዲወርሷት የሰጣቸውን ምድር ይወርሳሉ፡፡" (በጥቅስ ውስጥ የሚገኝ ጥቅስ የሚለውን ይጠቀሙ)

ህዝቡ

ይህ የእስራኤልን ህዝብ ያመለክታል፡፡ "የእስራኤል ህዝብ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

በሶስት ቀናት ውስጥ

እዚህ ስፍራ ያህዌ የሚገኝበትን ቀን እንደ መጀመሪያ ቀን እየቆጠረ ነበር፡፡ "ከአሁን በኋላ ሁለት ቀናት" ወይም "ከነገ በኋላ ባለው ቀን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡

ይህንን ዮርዳኖስን አቋርጡ

"አቋርጡ" የሚለው የሚያመለክተው ከወንዙ ወዲያ ማዶ መሻገርን ነው፡፡ "ከዮርዳኖስ ወንዝ ወዲያ ማዶ ተጓዙ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 1:12

አጠቃላይ መረጃ፡

የሮቤል፣ የጋድ እና የምናሴ ነገድ እኩሌታ ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተ ምስራቅ መቀመጥ መረጡ፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

የሮቤል ነገድ፡/ሮቤላዊያን

እነዚህ የሮቤል ትውልዶች ነበሩ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የጋድ ነገድ/ጋድአዊያን

እነዚህ የጋድ ትውልዶች ነበሩ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 1:14

አጠቃላይ መረጃ፡

ያህዌ ለሮቤላዊያን፣ ለጋድአዊያን እና ለምናሴ ነገድ እኩሌታ መናገሩን ቀጠለ

ልጆቻችሁ

"የእናንተ ትናንሽ ልጆች"

ከዮርዳኖስ ባሻገር

ይህ የሚያመለክተው ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተ መስራቅ ያለውን ስፍራ ነው፡፡ ቆይቶ ብዙዎቹ እስራኤላውያን ከዮርዳኖስ በስተ ምስራቅ ይኖራሉ፣ ስለዚህም ምስራቁን "ከዮርዳኖስ ማዶ" ብለው ይጠሩታል፡፡ በዚህ ጊዜ ግን ሁሉም ገና በስተ ምስራቅ ናቸው፡፡ "ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ወንድሞቻችሁ እረፍት እስኪያገኙ

ይህ እስራኤላውያን የሚይዟቸውን በከነዓን የሚኖሩ ጠላቶቻቸውን ሁሉ እንደሚያሸንፉ ያመለክተል፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እናንተ … ትወርሳላችሁ

ይህ በዚያ በምድሪቱ በሰላም እንደሚኖሩ ያመለክታል፡፡

ፀሐይ ከምትወጣበት፣ ከዮርዳኖስ ባሻገር

ይህ የዮርዳኖስን ምስራቃዊ ጎን ያመለክታል፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 1:16

አጠቃላይ መረጃ፡

ለኢያሱ የመለሱለት እነዚህ እስረኤላውያን፤ በተለይ ሮቤላዊያን፣ ጋድአዊያን እና ከምናሴ ነገድ እኩሌታዎቹ ነበሩ፡፡

በትዕዛዛትህ ላይ አመጹ፣ ደግሞም ቃልህን አልታዘዙም

እነዚህ ሁለት ሀረጋት በመሰረቱ ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፣ ደግሞም ማናቸውንም አይነት መልክ የያዘ አለመታዘዝ እንደሚያስቀጣ አጉልተው ይገልጻሉ፡፡ (ትይዩ ንጽጽራ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

ይገደላል

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ሞት እንፈርድበታለን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

በርታ ደግሞም ጽና

እስራኤል እና እግዚአብሔር፤ ኢያሱ ለእስራኤል ህዝብ መሪ ሆኖ እንዲቀጥል ሁለቱም ባህርያት አስፈላጊው እንደሆኑ ይቆጥራሉ፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 2

1 የነዌም ልጅ ኢያሱ፦ "ሄዳችሁ ምድሪቱን፥ በተለይም ኢያሪኮን ሰልሉ ብሎ ከሰጢም ሁለት ሰዎች በስውር ላከ። እነርሱም ሄደው ረዓብ ወደምትባል ሴተኛ አዳሪ ቤት ገቡ፥ በዚያም አደሩ። 2 ለኢያሪኮም ንጉሥ፦ እነሆ የእስራኤል ሰዎች አገሩን ሊሰልሉ ወደዚህ ገብተዋል ብለው ነገሩት። 3 የኢያሪኮም ንጉሥ፡-አገሩን ሁሉ ሊሰልሉ ወደ አንቺ የመጡትንና ወደ ቤትሽ የገቡትን ሰዎች አውጪ ብሎ ወደ ረዓብ መልእክት ላከ። 4 ነገር ግን ሴቲቱም ሁለቱን ሰዎች ወስዳ ሽሸገቻቸው። እርስዋም፦አዎን ሰዎቹ ወደ እኔ መጥተዋል፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ ሆኑ አላወቅሁም፤ 5 የከተማውም በር የሚዘጋበት ጊዜ ላይ ሰዎቹ ወጡ፤ ወዴት እንደ ሄዱ አላውቅም፤ፈጥናችሁ ከተከተላችሁ ምናልባት ልትይዙአቸው ትችላላችሁ አለች። 6 እርስዋ ግን ወደ ሰገንቱ አውጥታቸው፤ በዚያም በጣሪያ ውስጥ ባዘጋጀችው በተልባ እግር ውስጥ ሸሸጋቸው። 7 ሰዎቹ ወደ ዮርዳኖስ መሻገሪያ በሚወስደው መንገድ አሳደዱአቸው። አሳዳጆችም እንደወጡ በሮቹ ተቆለፉ። 8 ሰዎቹም ሳይተኙ ሴቲቱ ወደ እነርሱ ወደ ሰገነቱ ወጣች። 9 ሰዎቹንም እንዲህ አለቻቸው፦እግዚአብሔር ምድሪቱን አሳልፎ እንደሰጣችሁ እናንተንም መፍራት በላያችን እንደ ወደቀ፤ በምድሪቱም በሚኖሩት ሁሉ ከፊታችሁ እንደ ቀለጡ አውቃለሁ። 10 ከግብፅ ምድር በወጣችሁ ጊዜ እግዚአብሔር የኤርትራን ባሕር በፊታችሁ እንዳደረቀ፤ በዮርዳኖስም ማዶ በነበሩት እናንተም ፈጽማችሁ ባጠፋችኋቸው በሁለቱ በአሞራውያን ነገሥታት፥በሴዎንና በዐግ ያደረጋችሁትን ሰምተናል። 11 ይህን በሰማን ጊዜ ልባችን ቀለጠ፤ አምላካችሁም እግዚአብሔር በላይ በሰማይ በታችም በምድር እርሱ አምላክ ነውና ከእናንተ የተንሣ ከዚያ ወዲያ ለማንም ነፍስ አልቀርለትም። 12 እሁንም እባካችሁ እኔ ለእናንተ ቸርነት እንዳደረግሁ እናንተ 13 ደግሞ ለአባቴ ቤት ቸርነት እንድታደርጉ፥ አባቴንና እናቴን፥ ወንድሞቼንና እኅቶቼንና ቤተ ሰቦቻቸውን ሁሉ እንድታድኑ፤ እንዲሁም ከሞት እንድታድኑን በእግዚአብሔር ማሉልኝ እውነተኛ ምልክትም ስጡኝ። 14 ሰዎቹ፦ "ይህን ነገራችንን ባትገልጪ ነፍሳችን በነፍሳችሁ ፋንታ እስከሞት እንኳ ይሆናል፤ እግዚአብሔርም ምድሪቱን በሰጠን ጊዜ ምሕረትን እናደርጋለን እንዲሁም ታማኝ ሆነን እንገኛለን፤" አሉአት። 15 ቤትዋም በከተማ ቅጥር የተጠጋ ስለነበረ በመስኮቱ በገመድ አወረደቻቸው። 16 እርስዋም፦አሳዳጆቹ እንዳያገኙአችሁ ወደ ተራራው ሂዱ አሳዳጆቹም እስኪመለሱ ድረስ በዚያ ሦስት ቀን ተሰውራችሁ ተቀመጡ ኋላም መንገዳችሁን ትሄዳላችሁ አለቻቸው። 17 ሰዎቹም አሉአት፦ይህን የምንልሽን ካላደረግሽ እኛም ከዚህ ካማልሽን መሐላ የተነሣ የሰጠንሽን ተስፋ ከመጠበቅ ነፃ እንሆናለን። 18 እነሆ እኛ ወደ አገሩ በገባን ጊዜ ይህን ቀይ ክር እኛን ባወረድሽበት መስኮት በኩል እሰሪው ፤አባትሽንም እናትሽንም ወንድሞችሽንም የእባትሽንም ቤተ ሰብ ሁሉ ወደ አንቺ ቤት ሰብስቢ። 19 ከቤትሽም ደጅ ወደ ሜዳ የሚወጣ ሁሉ ደሙ በራሱ ላይ ይሆንበታል፤ እኛም ንጹሐን እንሆናለን። ነገር ግን ከአንቺ ጋር በቤቱ ውስጥ ያለውን አንድ ሰው ቢነካው ደሙ በእኛ ራስ ላይ ይሆናል። 20 ነገር ግን ይህንን ጉዳያችንን ብትገልጪ እኛም ከዚህ ካማልሽን መሐላ የተነሣ የሰጠንሽን ተስፋ ከመጠበቅ ነፃ እንሆናለን። 21 እርስዋም፦ እንደቃላችሁ ይሁን አለች። ሰደደቻቸውም እነርሱም ሄዱ፤ ቀዩንም ክር በመስኮቱ በኩል አንጠለጠልችው። 22 እነርሱም ሄደው ወደ ተራራው ደረሱ፥ አሳዳጆቹም እስኪመለሱ ድረስ እዚያ ለሦስት ቀናት ቆዩ። በመንገዱ ሁሉ ፈልገው አላገኙአቸውም። 23 ሁለቱም ሰዎች ተመለሱ፤ ከተራራውም ወርደው ተሻገሩ ወደ ነዌም ልጅ ወደ ኢያሱ መጡ፤ የደረሰባቸውንም ሁሉ ነገሩት። 24 ለኢያሱም እንዲህ አሉት፦ በእውነት እግዚአብሔር ይህን አገር ሁሉ በእጃችን አሳልፎ ሰጥቶናል፤ በአገሩም ውስጥ ያሉ ሰዎች ሁሉ ከእኛ የተነሣ እየቀለጡ አሉት።



Joshua 2:1

ነዌ

ይህ የኢያሱ አባት ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰጢም

ይህ በዮርዳኖስ ወንዝ ምስራቅ አቅጣጫ የሚገኝ ስፍራ ስም ነው፡፡ ትርጉሙ "የግራር ዛፎች" ማለት ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰላዮች

እነዚህ ሰዎች እስራኤላውያን ምድሪቱን እንዴት እንደሚወሯት መረጃ ለማግኘት የሄዱ ነበሩ፡፡

Joshua 2:4

አጠቃላይ መረጃ፡

ጋለሞታይቱ ረዓብ ሁለቱን እስራኤላውያን ሰላዮች ከጉዳት ጠበቀች፡፡

ነገር ግን ሴቲቱ ሁለቱን ሰዎች ወስዳ ደበቀቻቸው

ይህ የሆነው የንጉሡ መልዕክተኛ ከእርሷ ጋር ከመነጋገሩ አስቀድሞ ነው፡፡

ሴቲቱ

ይህ ጋለሞታይቱን ረዓብን ያመለክታል

ማምሻ/ለዐይን ያዝ ሲያደርግ

ቀኑ ወደ ምሽቱ ጨለማ መግባት የሚጀምርበት ጊዜ ነው

Joshua 2:6

ነገር ግን እርሷ … ወደ ሰገነቱ/ጣራ ላይ ወሰደቻቸው

ይህ ሰዎቹን እንዴት እንደ ደበቀቻቸው በኢያሱ 2፡4 ላይ ሚገኝ የመረጃ ዳራ እና ማብራሪያ ነው፡፡ (የመረጃ ዳራ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰገነት/ጣራ

ጣራው ጠፍጣፋ ጠንካራ ነበር፣ በመሆኑም ሰዎች በዙሪያው ሊረማመዱ ይችሉ ነበር

የተልባ እግር

ልብስ ለመስራት የሚውል፣ ክር/ቃጫ ለማግኘት የሚተከል ተክል፡፡

ሰዎቹ ተከተሏቸው

ሰዎቹ ሰላዮቹን የተከተሏቸው ረዓብ በኢያሱ 2፡5 ላይ ከነገረቻቸው የተነሳ ነው፡፡

መሻገሪያዎች/መልካ

የወንዝ ወይም ሌላ የውሃ አካል፣ በእርምጃ ወደ ሌላኛው ዳርቻ በእርምጃ ለመሻገር የሚቻልበት ጥልቀት የሌለው ስፍራ

Joshua 2:8

ገና ሳይጋደሙ

ይህ የሚያመለክተው በምሽቱ ወደ መኝታ መሄድን ነው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ያህዌ ምድሪቱን ለእናንተ እንደሰጣችሁ አውቃለሁ

"እናንተ" የሚለው ቃል የሚያመለክው መላውን የእስራኤል ሰዎች ነው፡፡ (እናንተ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮችን ይመልከቱ)

እናንተን መፍራት ወድቆብናል

ፈርተናል የሚለው የተገለጸው ፍርሃት ራሱ መጥቶ እንዳጠቃቸው ተደርጎ ነው፡፡ "እናንተን ፈራን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በፊታችሁ ቀለጥን

ይህ የፈራውን ህዝብ ከሚቀልጥና ከሚወርድ በረዶ ጋር ያነጻጽረዋል፡፡ አማራጭ ትርጉሞች ሊሆኑ የሚችሉት 1) በእስራኤላውያን ፊት ደካማ እንደሚሆኑ ወይም 2) እንደሚበታተኑ ነው፡፡ "እናንተን መቋቋም እስከማይችሉ ድረስ እጅግ ይፈራሉ" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 2:10

አጠቃላይ መረጃ፡

ረዓብ ከእስራኤላውያን ሰላዮች ጋር መነጋገሯን ቀጠለቸ

የደንገል/ቄጤማ ባህር

ይህ የቀይባህር ሌላው ስም ነው

ሴዎን…ዐግ

እነዚህ የአሞራውያን ነገሥታት ስሞች ናቸው፡፡(ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ልባችን ቀለጠ፣ አንዳች ድፍረት አልቀረልንም

እነዚህ ሁለት ሀረጋት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፣ በአንድ ላይ የቀረቡት ትኩረት ለመስጠት ነው፡፡ "ልባችን ቀለጠ" የሚለው ሃረግ የፈሩትን የኢያሪኮ ሰዎች ልብ እየቀለጠ ከሚወርድ በረዶ ጋር ነው ያነጻጽራል፡፡ (ጥንድ ትረጉም እና ዘይቤያዊ አነጋገር የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 2:12

አጠቃላይ መረጃ፡

ረዓብ ከእስራኤላውያን ሰላዮች ጋር መነጋገሯን ቀጠለቸ

እባካችሁ ማሉልኝ… እርግጠኛ የሆነ ምልክት ስጡኝ

እነዚህ ረዓብ ከሰለዮቹ እርግጠኛ የሆነ ምልክት መፈለጓን የሚገልጹ ተመሳሳይ ሃሳቦች ናቸው፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእናንተ መልካም ነበርኩ

"እናንተ" የሚለው ቃል ሁለቱን ሰላዮች ያመለክታል፡፡ (እናንተ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮችን ይመልከቱ)

ህይወታችንን አድኑ… ከሞት አድኑን

"አትግደሉን" የሚለውን ትሁት በሆነ መንገድ መግለጽ፡፡ (ዩፊሚዝም/የማያስደስትን ቃል ሻል ባለ ቃል መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 2:14

አጠቃላይ መረጃ፡

እስራኤላውያን ሰላዮች ረዓብ የጠየቀችውን በኢያሱ 2፡12 ቃል የገቡላትን ፈጸሙ

እስከ ሞት ድረስ እንኳን ቢሆን፣ ህይወታችንን ለእናንተ ህይወት ይህ ፈሊጥ ቃልኪዳናቸውን ካልጠበቁ እግዚአብሔር እርግማኑን በእነርሱ ላይ እንዲያመጣባቸው የሚምሉበት እና የሚጠይቁበት መንገድ ነው፡፡ "ቃል የገባነውን ሳናደርግ ብንቀር፣ ያህዌ እኛን ያጥፋን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 2:15

አጠቃላይ መረጃ፡

እስራኤላውያኑ ሰላዮች ከረዓብ ጋር መነጋገራቸውን ቀጠሉ፡፡

ይህንን ባታደርጊ

ይህ ሰላዮቹ ለረዓብ የገቡትን ቃል ኪዳን የሚፈጽሙበትን ሁኔታ ይገልጻል፡፡ "ይህ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው " ይህንን ደማቅ ቀይ ገመድ በመስኮቱ በኩል እሰሪው " የሚለውን በኢያሱ 2፡18 የሚገኘውን ነው፡፡ (መላምታዊ ሁኔታ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 2:18

አያያዥ ሃሳብ፡

እስራኤላውያኑ ሰላዮች በኢያሱ 2፡15 የገለጹትን ሁኔታ ያብራራሉ፡፡

አጠቃላይ መረጃ፡

እስራኤላውያኑ ሰላዮች ከረዓብ ጋር መነጋገራቸውን ቀጠሉ፡፡

ማናቸውም ከቤትሽ በር ውጭ የሄደ

ይህ ሃረግ መላምታዊ በመፍጠር አንድን ሁኔታ ይገልጻል፡፡ (መላምታዊ ሁኔታ የሚለውን ይመልከቱ)

ደሙ በራሳቸው ራስ ላይ ይሆናል

እዚህ ስፍራ "ደም" የሚለው የሚገልጸው የአንድ ሰውን መሞት ነው፡፡ ለራሳቸው ሞት ተጠያቂነቱ የተገለጸው ደም በራሳቸው ላይ እንደሚሆን ተደርጎ ነው፡፡ "ሞታቸው የገዛ ራሳቸው ጥፋት ይሆናል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት እና ዘይቤያዊ አገላለጽ የሚለውን ይመልከቱ)

እኛ በደለኞች አንሆንም

"ንጹሃን እንሆናለን"

በማንም ላይ እጅ ቢጫን

እዚህ ስፍራ "እጅ ቢጫን" የሚለው አንድ ሰው እንዲጎዳ ምክንያት መሆን በጨዋ አገላለጽ የተገለጸበት ነው፡፡ "በማንም ላይ ጉዳት እንዲደርስ ምክንያት ብንሆን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዩፊሚዝም/የማያስደስትን ቃል ሻል ባለ ቃል መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 2:20

አጠቃላይ መረጃ፡

ሁለቱ እስራኤላውያን ሰላዮች ከረዓብ ጋር መነጋገራቸውን ቀጠሉ፡፡

አጠቃላይ መረጃ፡

ሰላዮቹ ረዓብ ወደ እርሷ መምጣታቸውን እንዳትናገር ጠየቋት፣ ወይም ይህ ካልሆነ ቤተሰቧቿን ለማዳን ከገቡት መሃላ ነጻ ይሆናሉ፡፡

ብትናገሪ

"አንቺ" የሚለው ረዓብን ያመለክታል፡፡ (አንቺ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮችን ይመልከቱ)

እናንተ ያላችሁት ይደረግ

ረዓብ ቤተሰቧችዋ እንዲጠበቁ ከእነርሱ የመሃላ ቃል ጋር ተስማማች

Joshua 2:22

አጠቃላይ መረጃ፡

ሁለቱ እስራኤላውያን ኢያሪኮን ለቀው ወጡ፡፡

አሳዳጆቻቸው ተመለሱ

ወደ ኢያሪኮ ተመለሱ ማለቱ ሊረዳ ይችላል፡፡ "የእነርሱ አሳዳዶች ወደ ኢያሪኮ ከተማ ተመለሱ" በሚለው ውሰጥ እንደሚገኘው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አንዳች አላገኙም

ይህ የሚያመለክተው ሰላዮቹን ያላገኟቸውን ሰዎች ነው

Joshua 2:23

ሁለቱ ሰዎች ተመለሱ

ሁለቱ ሰዎች ወደ እስራኤላውያን ሰፈር ተመለሱ፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ዞረው፣ አቋርጠው ተመልሰው መጡ

እነዚህ እስራኤላውያን ወዳረፉበት ስፍራ መመለሳቸውን የሚገልጹ ተመሳሳይ አባባሎች ናቸው

አቋርጠው

"አቋርጠው" ማለት ከወንዙ ተቃራኒ ዳርቻ መሄድ ማለት ነው፡፡ "ከዚህኛው ዳርቻ ወደ ተቃራኒው የዮርዳኖስ ዳርቻ መሄድ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ነዌ

ይህ የወንድ ስም ነው፤ የኢያሱ አባት፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

እኛ

እዚህ ስፍራ "እኛ" የሚለው ቃል እስራኤልን ያመለክታል

የምድሪቱ ነዋሪዎች ቀለጡ

የምድሪቱ ነዋሪዎች ለእስራኤላዊያን ያላቸው አቋም ሲታይ በሙቀት እንደሚቀልጥ ነገር ይመስላል፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 3

1 ኢያሱም በጠዋት ተነሣ፥ እነርሱም ከሰጢም ተነሥተው ወደ ዮርዳኖስ መጡ፤ እርሱና የእስራኤልም ልጆች ሁሉ ሳይሻገሩም በዚም ሰፈሩ። 2 ከሦስት ቀንም በኋላ አለቆች በሰፈሩ መካከል ሄዱ። 3 ሕዝቡንም እንዲህ ብለው አዘዙ፦የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን ታቦት ሌዋውያን ካህናት ተሸክመውት ባያችሁ ጊዜ ከሰፈራችሁ ተነሥታችሁ መከትል አለባችሁ። 4 በእናንተና በታቦቱ መካከል ያለው ርቀት ሁለት ሺህ ክንድ ያህል ይሁን። በዚህ መንገድ በከዚሄ በፊት አልሄዳችሁበትምና የምትሄዱበትን መንገድ እንድታውቁ ወደ ታቦቱ አትቅረቡ። 5 ኢያሱም ለሕዝቡ እንዲህ አለ፦ እግዚእአብሔር በመካከላችሁ ድንቅ ነገር ያደርጋልና ነገ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር ቀድሱ። 6 ከዚያም ኢያሱ ካህናቱን እንዲህ አለ፦ የቃል ኪዳኑን ታቦት ተሸክማችሁ በሕዝቡ ፊት እለፉ። ስለዚህ የቃል ኪዳኑን ታቦት ተሸክመው በሕዝቡ ፊት አለፉ። 7 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ አለ፦ በዚህ ቀን በእስራኤል ሁሉ ፊት ከፍ ከፍ አደርጋለሁ። ከሙሴ ጋር እንደ ነበርሁ እንዲሁ ከእንተ ጋር መሆኔን ያውቃሉ። 8 አንተም የቃል ኪዳኑን ታቦት የሚሸከሙትን ካህናት፦ በዮርዳኖስ ውኃ ዳር ስትደርሱ በዮርዳኖስ ውስጥ ቁሙ ብለህ ታዛቸዋለህ። 9 ከዚያም ኢያሱ ለእስራኤል ሕዝብ እንዲህ አለ፦ ወደዚህ ቀርባችሁ የእግዚአብሔርን የአምላካችሁን ቃል ስሙ አለ። 10 ሕያው አምላክ በመካከላችሁ እንደ ሆነና እርሱም ኤዊያዊውንም ፈርዛዊውንም ጌርጌሳዊውንም አሞራዊውንም ኢያቡሳዊውንም ከፊታችሁ ፈጽሞ እንደሚያወጣ በዚህ ታውቃላችሁ። 11 እነሆ የምድር ሁሉ ጌታ የቃል ኪዳን ታቦት በፊታችሁ በዮርዳኖስ ውስጥ ያልፋል። 12 አሁምን ከእስራኤል ነገዶች አሥራ ሁለት ሰዎችን ምረጡ፤ ከየነገዱ አንድ አንድ ሰው ይሁን። 13 እንዲህም ይሆናል የምድርም ሁሉ ጌታ የእግዚአብሔርን ታቦት የተሸከሙ ካህናት የእግራቸው ጫማ በዮርዳኖስ ውኃ ሲቆም የዮርዳኖስም ውኃ ይቆማል፤ ከላይ የሚፈሰው ውኃ ሳይቀር መፍሰሱን ያቆማል፤ እንደ ክምርም ሆኖ ይቆማል። 14 ሕዝቡም ዮርዳኖስን ለመሻገር ከድንኳናቸው በወጡ ጊዜ የቃል ኪዳኑን ታቦት የተሸከሙ ካህናት በሕዝቡ ፊት ቀድመው ሄዱ። 15 የቃል ኪዳኑን ታቦት የተሸከሙ ወደ ዮርዳኖስ እንደመጡ፤ እግራቸውም የውኃውን ጫፍ በጠለቁ ጊዜ (በመከር ወራት ሁሉ ዮርዳኖስ እጅግ ሞልቶ እንደሚፈስ) 16 ከላይ የሚወርደው ውኃ ቆመ፤ በጻርታን አጠገብ ባለችው አዳም በምትባል ከተማ በሩቅ ቆሞ እንደ ክምርም ሆነ፤ ወደ ዓረባ ባሕር ወደ ጨው ባሕር የሚወርደውም ውኃ ፈጽሞ ተቋረጠ፤ ሕዝቡም በኢያሪኮ አጠገብ ተሻገሩ። 17 የእስራኤልም ሕዝቡ ሁሉ ዮርዳኖስን ፈጽመው አስኪሻሩ ድረስ የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት የተሸከሙ ካህናት በዮርዳኖስ መካክል በደረቅ መሬት ጸንተው ቆመው ነበር።



Joshua 3:1

ተነሱ

"ተነሱ" የሚለው ሃረግ "መንቃት" ማለት ነው፡፡

ሰጢም

እስራኤላውያን ወደ ተስፋ ምድራቸው ወደ ከነዓን ከመግባታቸው አስቀድሞ ከሰፈሩበት ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተ ምዕራብ በሞአብ ምድር የሚገኝ ስፍራ

Joshua 3:2

አለቆች

እነዚህ የማዘዝ ወይም ስልጣን ደረጃን የያዙ ሰዎች ናቸው

ሰዎች

ይህ የእስራኤል ህዝብ ነው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ሁለት ሺህ ክንድ

"2,000 ክንድ" ክንድ የሚለው ቃል ከክርን እስከ ጣት ጫፍ ድረስ ያለው እርቀት መለኪያ ነው፡፡ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ ርቀት እና ቁጥሮች የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 3:5

ራሳችሁን ቀደሱ

ይህ በያህዌ ፊት ንጹህ ለመሆን የሚደረግን ልዩ ዝግጅት ያመለክታል፡፡

ያህዌ ተአምራት ያደርጋል

ያህዌ ሁሉም የሚያየው እና የሚዳስሰው ተአምራት ያደርጋል

ታቦቱን ያዙ

ይህ ሌዋውያን ታቦቱን ከአንድ ስፍራ ወደ ሌላ ይዘው መሄዳቸውን ያመለክታል

Joshua 3:7

አጠቃላይ መረጃ፡

ካህናቱ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ያህዌ ለኢያሱ ነገረው፡፡

በመላው እስራኤል ዐይኖች ፊት ታላቅ ሰው አደርግሃለሁ

ዐይኖች የሚለው ማየትን ሲወክል ፣ ማየት የሚለው ማሰብን ወይም ፍርድን ይገልጻል፡፡ "ህዝቡ የማደርገውን ያያል፣ ደግሞም አንተን ታላቅ ሰው እንዳደረግኩህ ያስተውላሉ" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የዮርዳኖስ ውሃ ዳርቻ

ኢያሱ ወደ ዳርቻ ወይም ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ ደረሰ

Joshua 3:9

አጠቃላይ መረጃ፡

ያህዌ ምን ሊያደርግ እንደሆነ ኢያሱ ለእስራኤላውያን ነገራቸው፡፡ከፊታችሁ ሊያጠፋቸው ያህዌ በምድሪቱ የሚኖሩ ሌሎች ህዝቦችን ከምድሪቱ ይወጡ ዘንድ ወይም እንዲገደሉ ያደርጋል፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አቋርጠው

"አቋርጠው" ማለት ከወንዙ ተቃራኒ ዳርቻ መሄድ ማለት ነው፡፡ "ከዚህኛው ዳርቻ ወደ ተቃራኒው የዮርዳኖስ ዳርቻ መሄድ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 3:12

አጠቃላይ መረጃ፡

ያህዌ ምን ሊያደርግ እንደሆነ ኢያሱ ለእስራኤላውያን መናገሩን ቀጠለ፡፡

አጠቃላይ መረጃ

የእስራኤል አባቶች ቀይ ባህርን እንዳቋረጡ፣ እነዚህ ሰዎች ዮርዳኖስን በደረቅ ምድር ያቋርጣሉ

የእግራቸው ኮቴ

ይህ የሚያመለክተው የእግራቸውን ስር ነው

ከላይ የሚወርደው

ይህ ቃል የሚያመለክተው የዮርዳኖስ ወንዝ ውሃ ወደ እስራኤል የሚወርድበትን አቅጣጫ ነው

አንድ ክምር ሆኖ ቆመ

ውሃው በአንድ ነጥብ ወይም ስፍራ ላይ ይቆማል፡፡ ካህናቱ ዙሪያ አይፈስም

Joshua 3:14

የውሃ ዳርቻ፡

ይህ የውሃውን ገጽ እንዲሁም ውሃው ወደ ደረቅ ምድር የሚፈስበትን ዳርቻ ያመለክታል፡፡ (ስኔክቲኪ/ ዘይቤያዊ አነጋጋር- የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ፤ የሚለውን ይመልከቱ)አሁን ዮርዳኖስ ውሃ ሞልቶ እስከ መከር ጊዜ ድረስ ይፈስ ነበር ይህ የመረጃ ዳራ ያህዌ ሊያደርግ ያለውን አጉልቶ ያሳያል፡፡ (የመረጃ ዳራ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 3:17

አጠቃላይ መረጃ፡

ተአምራዊው የዮርዳኖስ ባህር መውረዱ ቀጠለ

ዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ የሚፈስበትን ያመለክታል፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

አቋረጡ

ይህ ሃረግ ከወንዙ ተቃራኒ ዳርቻ መሄድ ማለት ነው፡፡ "ከዚህኛው ዳርቻ ወደ ተቃራኒው ዳርቻ መሄድ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 4

1 ሕዝቡ ሁሉ ዮርዳኖስን ፈጽመው በተሻገሩ ጊዜ እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ አለ፦ 2 "ከሕዝቡ ከየነገዱ አንድ አንድ ሰው፥ አሥራ ሁለት ሰዎች ምረጥ። 3 እንዲህ ብለህ ትእዛዝ ስጣቸው፦"በዮርዳኖስ መካከል የካህናት እግር ከቆመበት ስፍራ አሥራ ሁለት ድንጋዮችን አንሡ፤ ተሸክማችሁም በዚህ ሌሊት በምታድሩበት ስፍራ አኑሩአቸው።" 4 ከዚያም ኢያሱ ከእያንዳንዱ የእስራኤል ነገድ አንድ አንድ ሰው የመረጣቸውን አሥራ ሁለት ሰዎች ጠራቸው። 5 ኢያሱም አላቸው፦"በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ታቦት ፊት በዮርዳኖስ መካከል፤ እያንዳንዱም ሰው በጫንቃው ከአንዳንድ ድንጋይ ጋር በእስራኤል ልጆች ሁሉ ነገድ ቁጥር አሥራ ሁለት ድንጋዮችን ተሸክመው ይለፉ። 6 ፤ልጆቻችሁም በሚመጣው ዘመን፦ እነዚህ ድንጋዮች ለእናንተ ምን ትርጉም አላቸው? ብለው በሚጠይቁበት ጊዜ ይህ በመካከላችሁ ምልክት ይሆናል። 7 በዚያን ጊዜ እናንተም እንዲህ ብላችሁ ትመልሳላችሁ፦ "በእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ፊት የዮርዳኖስ ውኃ ስለተቋረጠ ነው። በተሻገሩም ጊዜ የዮርዳኖስ ውኃ ቆመ፤ እነዚህም ድንጋዮች ለእስራኤል ልጆች ለዘላለም መታሰቢያ ይሆናሉ።" 8 የእስራኤልም ልጆች ኢያሱ እንዳዘዛቸው አደረጉ፤ እግዚአብሔርም ኢያሱን እንደ ተናገረው በእስራኤል ነገድ ቁጥር ከዮርዳኖስ መካከል እንደ እስራኤል ነገድ ቁጥር አሥራ ሁለት ድንጋዮች አንሥተው ወደሚያድሩበት ስፍራ ወሰዱ። በዚያም በሚያድሩበት ስፍራ አኖሩአቸው። 9 ኢያሱም የቃል ኪዳኑን ታቦት የተሸከሙ ካህናት እግሮች በቆሙበት ስፍራ በዮርዳኖስ መካከል ሌሎችን አሥራ ሁለት ድንጋዮች ተከለ። እስከ ዛሬም ድረስ መታሰቢያ ሆነው በዚያ አሉ። 10 ሙሴም ኢያሱን እንዳዘዘው ሁሉ እግዚአብሔር ኢያሱን ለሕዝቡ እንዲነገር ያዘዘው ነገር ሁሉ እስክፈጸም ድረስ ታቦቱን የተሸከሙ ካህናት በዮርዳኖስ መካከል ቆመው ነበር። ሕዝቡም ፈጥነው ተሻገሩ። 11 ሕዝቡም ሁሉ ፈጽመው መሻገራቸውን በጨረሱ ጊዜ የእግዚአብሔር ታቦትና ካህናቱ በሕዝቡ ፊት ተሻገሩ። 12 ሙሴም እንዳዘዘቸው የሮቤል ልጆች፥ የጋድም ልጆች፥ የምናሴም ነገድ እኩሌታ ተሰልፈው በእስራኤል ልጆች ፊት ተሻገሩ። 13 አርባ ሺህ ያህል ሰዎች ጋሻና ጦራቸውን ይዘው ለጦርነት በእግዚእብሔር ፊት ወደ ኢያሪኮ ሜዳ ተሻገሩ። 14 በዚያም ቀን እግዚአብሔር ኢያሱን በእስራኤል ሁሉ ፊት ከፍ አደረገው። ሕዝቡም ሙሴን እንዳከበሩት በዕድሜው ሁሉ አከበሩት። 15 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 16 "የምስክርን ታቦት የሚሸከሙትን ካህናት ከዮርዳኖስ እንዲወጡ እዘዝ።" 17 ኢያሱም ካህናቱን፦ ከዮርዳኖስ ውጡ ብሎ አዘዛቸው። 18 የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑን ታቦት የተሸከሙ ካህናት ከዮርዳኖስ መካከል በወጡ ጊዜና የካህናቱም እግር ጫማ ደረቅ መሬት መርገጥ በጀመረ ጊዜ የዮርዳኖስ ውኃ ወደ ስፍራው ተመለሰ፤ ቀድሞም ከአራት ቀናት በፊት እንደ ነበረ በዳሩርቻው ሁሉ መፍሰስ ጀመረ። 19 ሕዝቡም በመጀመሪያው ወር በአሥረኛው ቀን ከዮርዳኖስ ወጡ። ከኢያሪኮ በስተ ምሥራቅ በኩል በጌልገላ ሰፈሩ። 20 ከዮርዳኖስም ውስጥ የወሰዱአቸውን አሥራ ሁለቱን ድንጋዮች ኢያሱ በጌልገላ አቆማቸው። 21 ለእስራኤልም ልጆች እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፦ "በሚመጣው ዘመን ልጆቻችሁ አባቶቻቸውን፦ እነዚህ ድንጋዮች ምንድን ናቸው? ብለው ሲጠይቁ፥ 22 ለልጆቻችሁ እንዲህ ብላችሁ ታስታውቃላችሁ፦ እስራኤል ይህን ዮርዳኖስን በደረቅ ተሻገረ። 23 እስክንሻገር ድረስ አምላካችሁ የኤርትራን ባሕር ከፊታችን እንዳደረቀ እንዲሁ እስክትሻገሩ ድረስ አምላካችሁ እግዚአብሔር የዮርዳኖስን ውኃ ከፊታችሁ አደረቀ። 24 የእግዚአብሔርም እጅ ጠንካራ እንደ ሆነች የምድር አሕዛብ ሁሉ እንዲያውቁ አምላካችሁንም እግዚአብሔርን ለዘላለሙ እንድታከብሩ ነው።



Joshua 4:1

አጠቃላይ መረጃ፡

ምንም እንኳን ያህዌ በቀጥታ ለኢያሱ ቢናገርም፣ አንተ የሚለው በተጠቀሰ ጊዜ ሁሉ እስራኤልን ያጠቃልላል፡፡ (ተውላጠ ስም/የስም ምትክ የሚለውን ይመልከቱ)

አቋረጠ

"አቋረጠ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ከወንዙ ተቃራኒ ዳርቻ መሄድን ነው፡፡ "አቋርጦ ሄደ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የ ዮርዳኖስ

የዮርዳኖስ ወንዝ ፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእነርሱ ይህንን ተዕዛዝ ስጣቸው፡‘…'

በጥቅስ ውስጥ የተቀመጠው ቀጥተኛ እንዳልሆነ ጥቅስ ሊቀርብ ይችላል፡፡ "ካህናቱ በደረቅ ምድር ቀመውበት ከነበረበት ስፍራ ከዮርዳኖስ መሃል አስራ ሁለት ድንጋዮችን እንዲያነሱ ይህንን ትዕዛዝ ስጣቸው፣ እነዚያንም ድንጋዮች ይዘህ መጥተህ ዛሬ ምሽት በምታድርበት ስፍራ አኑራቸው" (በጥቅስ ውስጥ ጥቅስ እና ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ጥቅሶች የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 4:4

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ለአስራ ሁለቱ ሰዎች ምን ማድረግ እንዳለባቸው ነገራቸው፡፡ወደ ዮርዳኖስ መሃል እያንዳንዳችሁ በትከሻችሁ ድንጋይ ትሸከማላችሁ እያንዳንዳቸው አስራ ሁለቱ ሰዎች ከዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ ትልልቅ ድንጋይ አንስተው መተሰቢያ ለማኖር ወደ ሌላው ዳር ተሸክመው ወሰዱ፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 4:6

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ለእስራኤላውያን የአስራ ሁለቱ ድንጋዮች ክምር ትርጉሙ ምን እንደሆነ ነገራቸው

የዮርዳኖስ ውሃ በያህዌ የቃል ኪዳኑ ታቦት ፊት ተቋረጠ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ያህዌ የዮርዳኖስን ውሃ በቃል ኪዳኑ ታቦት ፊት አቋረጠው" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

የዮርዳኖስ ውሃዎች የነበሩት

"የዮርዳኖስ ወንዝ ነበር"

በታቦቱ ፊት ተቋርጠው ነበር

የዮርዳኖስ ወንዝ ካህናቱ ተሸክመውት እስከ ነበረው ታቦት ድረስ እንዳይፈስ እግዚአብሔር አግዶት ነበር

የዮርዳኖስ ውሃዎች ተቋርጠው ነበር

ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ቁልቁል ይፈስ የነበረው ውሃ በታቦቱ ፊት ቆመ፣ ስለዚህም ታቦቱን ጨምሮ ሁሉም በደረቀ የወንዝ መፋሰሻ ተጓዙ

Joshua 4:8

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ እና መላው እስራኤል ያህዌ እንዳዘዘው መስራታቸውን ቀጠሉ

ከዮርዳኖስ መሃል አስራ ሁለት ድንጋዮችን ተሸከሙ

ይህ የሚያመለክተው አስራ ሁለቱ ወንዶች ከዮርዳኖስ ወንዝ መፍሰሻ ድናጋዮችን መሸከማቸውን ነው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ከዚያ ኢያሱ በዮርዳኖስ መሃል አስራ ሁለት ድንጋዮች አስቀመጠ

እነዚህ አስራ ሁለቱ ሰዎች ከወንዙ መፋሰሻ የተሸከሟቸው ድንጋዮች ሳይሆኑ አስራ ሁለት ተጨማሪ ድንጋዮች ነበሩ፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

መታሰቢያው እስከ ዛሬ ድረስ በዚያ አለ

ይህ ማለት ጸሐፊው ይህንን መጽሐፍ እስከሚጽፍበት ቀን ድረስ መታሰቢያው በዚያ ነበር

Joshua 4:10

የ ዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስን ወንዝ ያመለክታል፡፡

ህዝቡ

ይህ የእስራኤልን ህዝብ ያመለክታል፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

አቋረጡ

ይህ ማለት ከወንዙ ተቃራኒ ዳርቻ መሄድ ነው፡፡ "ከዚህኛው ዳርቻ ወደ ተቃራኒው ዳርቻ መሄድ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በህዝቡ ፊት

ይህ የሚያመለክተው በህዝቡ ፊት መሆንን ወይም በሁሉም ህዝብ እይታ ውስጥ መሆንን ነው፡፡ እያንዳንዱ ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው አይቷል፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 4:12

የሮቤል ነገድ፣ የጋድ ነገድ እና የምናሴ ነገድ እኩሌታ በወታደራዊ አሰላለፍ በእስራኤል ህዝብ ፊት አለፉ

እነዚህ እስራኤላውያንን በዮርዳኖስ ወንዝ ምስራቅ ለማስፈር እና ጦርነቱን በመምራት ግዴታቸውን የሚወጡ የሶስቱ ነገዶች ወታደሮች ነበሩ፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ልክ እነርሱ

"እነርሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእስራኤልን ህዝብ ነው

ሙሴን አከበሩት

ይህ ማክበርን ብቻ የሚያመለክት አይደለም፣ ነገር ግን ሙሴን ሲከተሉ ያደርጉት እንደነበረው ለእርሱ ትዕዛዛት መገዛትን እና እርሱን እንደ ሰራዊቱ አዛዥ መቀበልን ጭምር ያመለክታል፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 4:17

አጠቃላይ መረጃ፡

ጸሐፊው ለቀደመው ትውልድ የዮርዳኖስን ወንዝ መክፈል ቀይ ባህርን ከመክፈል ልዩነት እንደሌለው ግልጽ እያደረገ ነበር የዮርዳኖስ ውሃ ወደ ቦታው ተመልሶ በዳርቻዎቹ ሞልቶ ፈሰሰ የዮርዳኖስ ወንዝ እስራኤላውያን በደረቅ ምድር ከማለፋቸው በፊት እና በኋላም በዳርቻዎቹ ሞልቶ ይፈስና አካባቢውን ያጥለቀልቅ ነበር አራት ቀናት "4 ቀናት" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 4:19

ከዮርዳኖስ ወጡ

ይህ እስራኤል የዮርዳኖስ ወንዝን በደረቅ ምድር ማቋረጣቸውን ያመለክታል፡፡በአራተኛው ወር በአስረኛው ቀን ይህ በዕብራውያን ቀን አቋጣጠር የመጀመሪያው ወር ነው፡፡ አስረኛው ቀን በምዕራባውያን ቀን አቋጣጣር በመጋት መጨረሻ አቅራቢያ ነው፡፡ (የዕብራውያን ወራት እና ተከታታይ ቁጥሮች የሚሉትን ይመልከቱ)

ከዮርዳኖስ ወንዝ ውስጥ ያወጧቸው አስራ ሁለቱ ድንጋዮች ኢያሱ በደረቅ ምድር የመሻገራቸውን መታሰቢያ መገንባት ይችል ዘንድ እያንዳንዱ ነገድ ከዮርዳኖስ ወንዝ አንድ ድንጋይ መውሰድ ነበረበት፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 4:22

አጠቃላይ መረጃ

ኢያሱ ለህዝቡ ስለ ድንጋይ ክምሩ ማስታወሱን ቀጠለ፡፡ ለልጆቻችሁ ንገሩ እስራኤላውያን ልጆቻቸው ያህዌን ለዘለዓለም ያከብሩ ዘንድ የእግዚአብሔርን ተአምራቶች ለእነርሱ ማስተማር ነበረባቸው፡፡ የያህዌ እጅ ታላቅ ነው ይህ የያህዌ ሃይል ታላቅ መሆኑን ያመለክታል፡፡ "ያህዌ ታላቅ ነው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 5

1 በዮርዳኖስ ማዶ በምዕራብ በኩል የነበሩ የአሞራውያን ነገሥታት ሁሉ፥ በታላቁም ባሕር አጠገብ የነበሩ የከነዓናውያን ነገሥታት ሁሉ፥ የእስራኤል ሕዝብ እስኪሻገሩ ድረስ የዮርዳኖስን ውኃ እግዚአብሔር እንዳደረቀ በሰሙ ጊዜ ልባቸው ቀለጠ፤ ከእስራኤልም ሕዝብ የተነሣ የአንድም ሕዝብ ነፍስ አልቀረላቸውም። 2 በዚያን ጊዜ እግዚአብሔር ኢያሱን እንዲህ አለው፦"የባልጩት ድንጋይ ስለት ሠርተህ የእስራኤልን ሕዝብ እንደገና ግርዛቸው።" 3 ኢያሱም የባልጩት ድንጋይ ስለት ሠርቶ ግብት ሃራሎት (ትርጉሙም የግርዛት ኮረብታ) በተባለ ስፍራ የእስራኤልን ወንዶች ሁሉ ገረዛቸው። 4 ኢያሱም የገረዘበት ምክንያት ይህ ነው፤ ከግብፅ የወጡት ወንዶች ሁሉ ጦረኞችን ሁሉ ጭምር ከግብፅ ከወጡ በኋላ በመንገድ ላይ በምድረ በዳ ሞቱ። 5 የወጡት ሕዝብ ሁሉ ተገርዘው ነበር፤ ነገር ግን ከግብፅ በወጡበት መንገድ በምድረ በዳ የተወለዱት ሕዝብ ሁሉ አልተገረዙም ነበር። 6 ከግብፅ የወጡ የእስራኤል ሕዝብና ጦረኞች ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ባለመስማታቸው እስኪሞቱ ድረስ አርባ ዓመት በምድረ በዳ ይጓዙ ነበር ። እግዚአብሔርም ወተትና ማር የምታፈስሰውን ምድር ለእኛ ይሰጠን ዘንድ ለአባቶቻቸው የማለላቸውን ምድር እንደማያሳያቸው ማለላቸው። 7 እግዚአብሔር በእነርሱ ፋንታ ያስነሳቸው በመንገድ ሳሉ ሳይገረዙ የነበሩ ኢያሱም ገረዛቸው እነዚህን ልጆቻቸው ነበሩ። 8 ሕዝቡም ሁሉ በተገዙ ጊዜ እስኪድኑ ድረስ በሰፈር ውስጥ በየስፍራቸው ነበሩ። 9 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ አለ፦ ዛሬ የግብፅን ነውር ከእናንተ ላይ አንከባልያለሁ አለው፤ ስለዚህ የዚያ ስፍራ ስም እስከ ዛሬ ድረስ ጌልገላ ተብሎ ይጠራል። 10 የእስራኤልም ሕዝብ በጌልገላ ሰፈሩ። ከወሩም በአሥራ አራተኛው ቀን በመሸ ጊዜ በኢያሪኮ ሜዳ ፋሲካ አደረጉ። 11 ከፋሲካውም በዓል ቀን በኋላ በዚያው ዕለት የምድሪቱን ፍሬ ቂጣና ቆሎ በሉ።. 12 ከምድሪቱም ፍሬ ከበሉበት ቀን በኋላ መና ተቋረጠ። ከዚያም ጊዜ ጀምሮ ለእስራኤል ልጆች መና አልነበራቸውም፤ ነገር ግን በዚያ ዓመት የከነዓንን ምድር ፍሬ በሉ። 13 ኢያሱ ወደ ኢያሪኮ አጠገብ በነበረ ጊዜ ዓይኖቹን አንሥቶ ተመለከተ፥ እነሆም ሰይፍ በእጁ የያዘ ሰው በፊቱ ቆሞ ነበር፤ ኢያሱም ወደ እርሱ ቀርቦ፦ ከእኛ ወገን ወይስ ከጠላቶቻችን ወገን ነህን? አለው። 14 እርሱም፦ አይደለሁም እኔ የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ሆኜ እዚህ መጥቼአለሁ አለ። ኢያሱም ወደ ምድር በግምባሩ ተደፍቶ ሰገደና፦ ጌታዬ ለአገልጋዩ የሚነግረው ምንድን ነው? አለው። 15 የእግዚአብሔርም ሠራዊት አለቃ ኢያሱን፦ አንተ የቆምህበት ስፍራ የተቀደሰ ነውና ጫማህን ከእግህ አውልቅ አለው። ኢያሱም እንዲሁ አደረገ።



Joshua 5:1

ልቦቻቸው ቀለጡ … በውስጣቸው ነፍስ አልቀረም ነበር

እነዚህ ሁለት ሃረጎች በመሰረቱ ተመሳሳይ ትርጉም ሲኖራቸው የፍርሃታቸውን ጥልቀት ያጎላሉ፡፡ (ትይዩ ተነጻጻሪ ዘይቤ/ፓራራሊዝም የሚለውን ይመልከቱ)

ልቦቻቸው ቀለጡ

እዚህ ስፍራ "ልቦች" የሚለው ድፍረትን ያመለክታል፡፡ ሰም በእሳት እንደሚቀልጥ ድፍረታቸው ቀልጦ ጠፍቶ እጅግ ፈርተው ነበር፡፡ "ድፍረታቸውን ሁሉ አጡ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት እና ዘይቤያዊ አነጋገር የሚሉትን ይመልከቱ)በውስጣቸው ነፍስ አልቀረም ነበር እዚህ ስፍራ "ነፍስ" የሚለው የሚያመለክተው ለመዋጋት ያላቸውን ፈቃድ ነው፡፡ "ለመዋጋት አንዳች ፈቃድ አልነበራቸውም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 5:2

ኢያሱ የባልጩት ምላጭ አዘጋጀ… ወንዶቹን ሁሉ ገረዘ

ከ600,000 በላይ ወንዶች ነበሩ፣ ስለዚህም ኢያሱ በዚህ ተግባር ላይ በነበረበት ጊዜ ሌሎች ብዙ ሰዎች እንደረዱት ግልጽ ነው፡፡ ይህ አንባቢውን ግራ የሚያጋባው ከሆነ፣ ተርጓሚው ይህንን ግልጽ ማድረግ ሊያስፈልገው ይችላል፡፡ "ኢያሱ እና እስራኤላውያኑ ራሳቸው የባልጩት ምላጭ አዘጋጅተው… ወንዶችን ሁሉ ገረዙ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ጊብዓዝ ዓረሎት

ይህ እስራኤል ራሳቸውን ለያህዌ ዳግም መስጠታቸውን የሚታወስበት ስፍራ ስም ነው፡፡ ትርጉሙ "የሸለፈት ኮረብታ" ማለት ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 5:4

አጠቃላይ መረጃ

የእስራኤል ወንዶች ሁሉ የሚገረዙበት ምክንያት ተገልጽዋል፡፡

የጦር ሰዎች

ወታደር ለመሆን እድሜያቸው የደረሰ ወንዶች

Joshua 5:6

የያህዌን ድምጽ ታዘዙ

እዚህ ስፍራ "ድምጽ" የሚለው የሚያመለክተው ያህዌ የተናገራቸውን ነገሮች ነው፡፡ "ያህዌ ያዘዛቸውን ነገሮች ታዘዙ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)ወተት እና ማር የምታፈስ ምድር ምድሪቱ ወተት እና ማር ከእነዚያ እንስሳት እና ተክሎች በምድሪቱ እንደሚፈስ፣ ለእንስሳት እና ተክሎች መልካም እንደሆነች እግዘአብሔር ተናገረ፡፡"ከብቶችን ለማርባት እና እህል ለማብቀል እጅግ መልካም ሆነች ምድር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር እና ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 5:8

በዚህ ዕለት የግብጽን ውርደት ከላያችሁ አንከባልያለሁ

ውርደታቸው የተገለጸው መንገዳቸውን እንደዘጋ ትልቅ ድናጋይ/ቆጥኝ ተደርጎ ነው፡፡ እዚህ ስፍራ "አንከባልላለሁ" የሚለው "ማስወገድ" የሚል ትርጉም አለው፡፡ "በዚህ ዕለት የግብጽን ውርደት ከእናንተ ላይ አስወግጃለሁ" ወይም "በግብጽ ባሮች በነበራችሁ ጊዜ ተዋርዳችሁ ነበር፡፡ ዛሬ ግን፣ ከእንግዲህ የተዋረዳችሁ እንዳትሆኑ አድርጌያችኋለሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 5:10

በወሩ አስራ አራተኛ ቀን

ይህ በምዕራባውያን ቀን አቆጣጠር ወደ መጋቢት መጨረሻ ነው፡፡ "የመጀመሪያው ወር አስራ አራተኛ ቀን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (የዕብራውያን ቀን አቆጣጠር እና ተከታታይ ቁጥር እንዲሁም ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 5:13

ዐይኖቹን አንስቶ ወደ ላይ ሲመለከት እነሆ፣ አንድ ሰው ቆሞ አየ

እዚህ ስፍራ ወደላይ አነሳ የሚለው የተነገረው ኢያሱ በቀጥታ ዐይኖቹን በእጆቹ እንዳነሳ ተደርጎ ነው፡፡ "አቅንቶ ሲመለከት አንድ ሰው ቆሞ አየ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር

እነሆ

"እነሆ" የሚለው ቃል ለአዲስ መረጃ ልዩ ትኩረት እንድንሰጥ ያነቃናል፡፡ እርስዎ የሚተረጉሙበት ቋንቋ ይህን የሚተረጉምበት የራሱ መንገድ ሊኖረው ይችላል፡፡

ሰይፉን መዞ በእጆቹ ይዞ ነበር

እዚህ ስፍራ "እርሱ" እና "የእርሱ" የሚሉት ቃላት ሚያመለክቱት ከኢያሱ ፊት የቆመውን ሰው ነው፡፡

Joshua 5:14

እርሱ አለ

"እርሱ" የሚለው ቃል ኢያሱ ያየውን ሰው ያመለክታል፡፡

ከየትኛሁም

ይህ ሰውየው ለኢያሱ ጥያቄ መልስ መስጠት የጀመረበት ነው፣ "አንተ ከእኛ ወይስ ከጠላቶቻችን ጋር ነህ?" ይሀ አጭር መልስ ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ "እኔ ከእናንተም ሆነ ከጠላቶቻችሁ ከየትኛውም ወገን አይደለሁም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ ኢያሱ በአምልኮ ወደ ምድር ተደፋ ይህ የአምልኮ ድርት ነበር፡፡ (ትምዕርታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ) ጫማህን ከእግርህ አውልቅ ይህ የውዳሴ/አምልኮ ድርጊት ነበር፡፡ (ትምዕርታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 6

1 ከእስራኤልም ሠራዊት የተነሣ የኢያሪኮ በሮች መጽሞ ተዘግተው ነበር። ወደ እርስዋም የሚገባና የሚወጣ ማንም አልነበረም። 2 እግዚአብሔርም ኢያሱን አለው፦ ተመልከት፥ ኢያሪኮንና ንጉሥዋን የሠለጠኑ ወታደሮችዋንም በእጅህ አሳልፌ ሰጥቼአለሁ። 3 ሠራዊቶኞቻችሁ ሁሉ ከተማይቱን አንድ ጊዜ መዞር አለባቸው። ይህንንም ለስድስት ቀናት አድርጉት። 4 ሰባትም ካህናት ሰባት ቀንደ መለከት በታቦቱ ፊት ይሸከሙ፤ በሰባተኛውም ቀን ከተማይቱን ሰባት ጊዜ ይዙሩ፥ ካህናቱም ቀንደ መለከቱን ይንፉ። 5 ቀንደ መለከቱም ባለማቋረጥ ሲነፋ የመለከቱንም ድምፅ በሰማችሁ ጊዜ ሕዝቡ ሁሉ ታላቅ ጩኸት ይጩኽ፥ የከተማይቱም ቅጥር ይወድቃል። እያንዳንዱ ወታደር ወደፊት በመሄድ ማጥቃት አለባቸው። 6 ከዚያም የነዌ ልጅ ኢያሱ ካህናቱን ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ የቃል ኪዳኑን ታቦት ተሸከሙ፥ ሰባትም ካህናት ሰባት ቀንደ መለከት ወስደው በእግዚአብሔር ታቦት ፊት ይሂዱ አላቸው። 7 ሕዝቡንም፦ ሂዱ፥ ከተማይቱንም ዙሩ፥ሠራዊቱም በእግዚአብሔር ታቦት ፊት ይሂዱ አለ። 8 ኢያሱም ለሕዝቡ እንደተናገረው ሰባቱ ካህናት ሰባቱን ቀንደ መለከት በእግዚአብሔር ታቦት ፊት ይዘው ወደፊት እያለፉ ቀንደ መለከቱንም ይነፉ ነበር። የእግዚአብሔርም ቃል ኪዳን ታቦት ከኋቸው ይከተላቸው ነበር። 9 ሠራዊቱም በካህናቱ ፊት ቀንደ መለከታቸውን እየነፉ ይሄዱ ነበር፤ ከዚያም ከቃል ኪዳን ታቦት ኋላ ደጀን ጦር ይሄድ ነበር፤እንዲሁም ካህናቱ ቀንደ መለከታቸውን ያለማቋረጥ ይነፉ ነበር። 10 ኢያሱ ግን ሕዝቡን እንዲህ ብሎ አዘዛቸው፦ እኔ ጩኹ እስከምልበት ቀን ድረስ አትጩኹ፥ ከአፋችሁም ድምፅ አይውጣ፤ በዚያን ጊዜ ብቻ ትጮኻላችሁ። 11 ስለዚህ እግዚአብሔር የዚያን ቀን የቃል ኪዳን ታቦት አንድ ጊዜ ከተማይቱን እንዲዞር አደረገው፤ ከዚያም ወደ ማደሪያቸው ገቡ፤ ሌሊቱንም እዚያው አደሩ። 12 ከዚያም ኢያሱ ማለዳ ተነሣ ካህናቱም የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን ታቦት ተሸከሙ። 13 ሰባቱም ካህናት ሰባት ቀንደ መለከት ይዘው በእግዚአብሔር ታቦት ፊት በቀስታ እየሄዱ ቀንደ መለከቱንም ይነፉ ነበር። ሠራዊቱም በፊታቸው ይሄዱ ነበር። የደጀን ጦር ከእግዚአብሔር ታቦት ኋላ በሚድበት ጊዜ የቀንደ መለከት ድምፅ ያልማቋረጥ ይሰማ ነበር። 14 በሁለተኛውም ቀን ከተማይቱን አንድ ጊዜ ዞረው ወደ ሰፈር ተመለሱ፤ ስድስት ቀንም እንዲሁ አደረጉ። 15 በሰባተኛውም ቀን ሲነጋ ማልደው ተነሡ፥ ከዚህ በፊት በተለመደው ሁኔታ ከተማይቱን ሰባት ጊዜ ዞሩ፤ ከተማይቱን ሰባት ጊዜ የዞሩት በዚያ ቀን ነው። 16 በሰባተኛውም ቀን ካህናቱ ቀንደ መለከቱን ሲነፉ ኢያሱ ሕዝቡን አዘዘ፦ እግዚአብሔር ከተማይቱን ሰጥቶአችኋልና ጩኹ። 17 ከተማይቱና በእርስዋም ያለው ሁሉ ለእግዚአብሔር የተለየና ለጥፋት ይሆናሉ። የላክናቸውን መልክተኞች ስለ ሸሸገች ሴተኛ አዳሪዋ ረዓብ ብቻና ከእርስዋም ጋር በቤትዋ ውስጥ ያሉት ሁሉ በሕይወት ይኖራሉ። 18 እናንተ ግን ለጥፋት የተለዩ ነገሮችን ከለያችሁት በኋላ አንዳች እንዳትወስዱ ራሳችሁን ጠብቁ። ለጥፋትም ከሆነው ነገር አንዳች የወሰዳችሁ እንደ ሆነ የእስራኤልን ሰፈር እንዲጠፋ ታደርጉታላችሁ፥ ችግርም ታመጣላችህ። 19 ብር፥ ወርቅ፥ ናስና ከብረት የተሠሩ ዕቃዎች ሁሉ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ይሁን። ወደ እግዚአብሔርም ግምጃ ቤት ይግባ። 20 ሕዝቡም ጮኹ፥ ካህናቱም ቀንደ መለከቱን ነፉ። ሕዝቡም የቀንደ መለከቱን ድምፅ በሰሙ ጊዜ ታልቅ ጩኸት ጮኹ፥ ቅጥሩም ሲወድቅ፤ ሕዝቡም እያንዳንዱ አቅንቶ ወደ ፊቱ ወደ ከተማይቱ ወጣ፤ ከተማይቱንም ያዙ። 21 በከተማይቱም የነበሩትን ሁሉ ወንዱንና ሴቱን፥ ሕፃኑንና ሽማግሌውን፥ በሬውንም ፥በጉንና አህያውን በሰይፍ ስለት ፈጽመው አጠፉ። 22 ኢያሱም ምድሪቱን የሰለሉትን ሁለቱን ሰዎች እንዲህ አላቸው፦ ወደ ሴተኛ አዳሪዋ ቤት ግቡ ከዚያም ሴቲቱንና ከእርስዋ ጋር ያሉትን ሁሉ እንደ ማላችሁላት አውጡ። 23 ሰላዮቹም ወጣቶች ሄደው ረዓብን አውጧአት፤ አባትዋንና እናትዋን፥ ወንድሞችዋንም፥ አብሯት የነበሩ ቤተ ዘምዶችዋንም ሁሉ አወጡ። ከእስራኤልም ሰፈር ውጭ ወዳለው ስፍራ አመጦአቸው። 24 ከተማይቱንም በእርስዋም የነበረውን ሁሉ በእሳት አቃጠሉ። ብሩ፥ ወርቅ፥የናሱና የብረት ዕቃዎች ብቻ በእግዚአብሔር ግምጃ ቤት አስቀመጡአቸው። 25 ነገር ግን ኢያሪኮን ሊሰልሉ ኢያሱ የሰደዳቸውን መልክተኞች የሸሸገች ሴተኛ አዳሪዋን ረዓብን፥ የአባትዋንም ቤተ ሰብ፥አብሯት የነበሩትንም ሁሉ ኢያሱ በሕይወት እንዲሆሩ ፈቀደላቸው። እርስዋም ኢያሱ ኢያሪኮን እንዲሰልሉ የላካቸውን ሰዎች ስለሸሸገች በእስራኤል መካከል እስከ ዛሬ ድረስ ትኖራለች። 26 በዚያን ጊዜም ኢያሱ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፦ ይህችን ኢያሪኮ ከተማን ለመሥራት የሚነሣ ሰው በእግዚአብሔር ፊት የተረገመ ይሁን። መሠረትዋን ሲጀምር በኩር ልጁ ይሙት፥ እርዋንም ሲያቆም ታናሹ ልጁ ይሙት፥ ብሎ ማለ። 27 እግዚአብሔርም ከኢያሱ ጋር ነበር፤ ዝናውም በምድር ሁሉ ላይ ወጣ።



Joshua 6:1

አሁን

ይህ ቃል እዚህ ስፍራ ያገለገለው ዋናው የታሪክ መስመር ሌላ መስመር እንዲከተል ነው፡፡እዚህ ላይ ተራኪው የኢያሪኮ በሮች ለምን እንደተዘጉ እና እንደተቆለፉ ይነግረናል፡፡

ኢያሪኮን፣ ንጉሥዋን፣ እና የሰለጠኑ ወታደሮችዋን በእጃችሁ አሳላፌ ሰጥቻችኋለሁ

ያህዌ ለኢያሱ ይህንን በእርግጥ እንደሚያደርግ የሚነግረው አስቀድሞ ነገሩ ያደረገው መሆኑን በመግለጽ ነው፡፡ (ሃላፊ የትንቢት ጊዜ የሚለውን ይመልከቱ)

በእጆችህ

"እጅ" የሚለው ቃል እጅ የሚፈጽመውን ለመቆጣጠር የሚውል ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት/ ነው፡፡ "ስለዚህ አንተ ይህንን መፈጸም ትችላለህ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 6:3

አያያዥ ሃሳብ፡

እግዚአብሔር ለኢያሱ ህዝቡ ማድረግ ያለበትን መናገሩን ቀጠለ

ይህንን ለስድሰት ቀናት ማድረግ አለባችሁ

"ይህንን ለስድስት ቀናት በየዕለቱ በቀን አንዴ ማድረግ አለባችሁ"

ሰባት ካህናት በታቦት ፊት ሰባት ቀንደ መለከት መያዝ አለባቸው

ሰባቱ ካህናት ታቦቱን ከያዙና በከተማይቱ ዙሪያ ከሚጓዙ ሌሎች ካህናት ፊት ይሂዱ

Joshua 6:5

አያያዥ ሃሳብ፡

እግዚአብሔር ለኢያሱ ህዝቡ ማድረግ ያለበትን መናገሩን ቀጠለ

እነርሱ የመለከቱን… ድምጽ ከፍ አድርገው ይንፉት

"እነርሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሰባቱን ካህናት ነው "ቀንደ መለከት" እና "መለከት" የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት በኢያሱ 6፡4 የተጠቀሰውን ካህናቱ የሚነፉትን ቀንደ መለከት ነው

የከተማይቱ ቅጥር

"የከተማይቱ ውጫዊ ቅጥር" ወይም "ከተማይቱ የታጠረችበት ገንብ"

Joshua 6:6

ነዌ

የኢያሱ አባት ነው፡፡(ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የቃል ኪዳኑን ታቦት ያዙ

"የቃል ኪዳኑን ታቦት ይዛችሁ ተጓዙ)

Joshua 6:8

በያህዌ ፊት

አማራጭ ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) "ያህዌን በመታዘዝ" ወይም 2) በያህዌ ታቦት ፊት ለፊት" (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ድምጸ መለከቶቹን ከፍ አድርገው ነፉ

x

Joshua 6:10

ምንም ድምጽ ከአፋችሁ አይውጣ

ከአንድ ሰው አፍ የሚወጣ ድምጽ የሚያመለክተው የዚያን ሰው ንግግር ወይም ጩኸት ነው፡፡ "አትጩሁ ወይም አትናገሩ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ኢያሱ ግን ህዝቡን አዘዘ

ኢያሱ ህዝቡን ከተማዋን መዞር ከመጀመራቸው አስቀድሞ አዘዛቸው፡፡ "ኢያሱ ህዝቡን አዝዞ ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (የድርጊቶች ቅደም ተከተል የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 6:12

ሰባት ካህናት … ሰባት ድምጸ መለከቶች

"7 ካህናት… 7 ድምጸ መለከቶች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በመለከቶቹ ከፍ ያለ ድምጽ አሰሙ

ይህ ማለት ድምጸመለከቶቻቸውን ከፍ ያለ ድምጽ እንዲያሰሙ አድርገው ደጋግመው ነፉ ማለት ነው፡፡ "ያለማቋረጥ ድምጸ መለከቶቹ ከፍ ያለ ድምጽ እንዲያሰሙ አደረጉ" ወይም "ያለ ማቋረጥ ድምጸ መለከቶቹን ነፉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡

በሁለተኛው ቀን

በሚቀጥለው ዕለት (ተከታታይ ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ) እነርሱ ይህንን አደረጉ እስራኤል በኢያሪኮ ዙሪያ በእየለቱ አንድ ጊዜ ዞሩ

ስድስት ቀናት

"6 ቀናት" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 6:15

ህዝቡ

ይህ የእስራኤልን ህዝብ ያመለክታል

መለከቶቹን ከፍ ባለ ድምጽ ነፉ

"ድምጸ መለከቶቹን ከፍ አድርገው ነፉ" ወይም "ድምጸ መለከቶቹን ነፉ"

ያህዌ ለእናንተ ሰጥቷችኋል

ኢያሱ ያህዌ ከተማዋን በእርግጥ ለእነርሱ እንደሚሰጥ ነገሩ ከመሆኑ አስቀድሞ እንደተፈጸመ እየተናገረ ነው፡፡ (ኃላፊ የትንቢት ጊዜ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰጥቷችኋል

"እናንተ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው መላውን የእስራኤል ህዝብ ነው፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መገለጫ መልኮች ይመልከቱ)

Joshua 6:17

አያያዥ ሃሳብ፡

ኢያሱ ለእስራኤል ህዝብ መናገሩን ቀጠለ

ከተማይቱ እና በውስጧ የሚኖሩ ሁሉ ይጠፉ ዘንድ ለያህዌ የተለዩ ይሆናሉ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ከተማይቱን እና በውስጣ የሚኖሩትን ሁሉ ይጠፉ ዘንድ ለያህዌ መለየት አለባችሁ" ወይም " ከተማቱን እና በውስጧ ሚኖሩትን ሁሉ በማጥፋት ለያህዌ መለየት አለባችሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

አንዳች ነገር እንዳትወስዱ ተጠንቀቁ

መጠንቀቅ የሚለው የተገለጸው ራሳቸውን መጠበቅ እንዳለባቸው ተደርጎ ነው፡፡ "ነገሮቹን አለመውሰዳችሁን ጥንቃቄ አድርጉ" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በዚያ ነገር ችግር ታመጣላችሁ

በከተማይቱ ላይመጥፎ ነገር እንዲፈጠር አንዳች ነገር ማድረግ የተገለጸው በላይዋ ላይ ችግር ማምጣት በሚል ነው፡፡ "በእርሷ ላይ መጥፎ ነገር እንዲደርስ ምክንያት ትሆናላችሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የያህዌ ሃብት

ያህዌን ለማምለክ የተለዩ ነገሮች ስብስብ

Joshua 6:20

ህዝቡ በታላቅ ድምጽ ጮኸ

"የእስራኤል ሰዎች ጮኹ"

በመለከቶች ታላቅ ድምጽ አሰሙ

"መለከቶቹን ከፍ አድረገው ነፉ" ወይም "ቀንደ መለከቶቹን ነፉ"

በሰይፍ ስለት በከተማይቱ ውስጥ የነገረውን ሁሉ ሙሉ ለሙሉ አጠፉ

"የሰይፍ ስለት" የሚለው የሚገልጸው ወታደሮች በጦርነት ውስጥ የሚጠቀሙባቸውን ሰይፎች እና ሌሎች መሳሪያዎች ነው፡፡ "በሰይፎቻቸው በከተማይቱ ውስጥ የሚገኙትን ሁሉ ሙሉ ለሙሉ አጠፉ" (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ ሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 6:23

ከተማይቱን አቃጠሉ

"እነርሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው እስራኤላውያን ወታደሮችን ነው፡፡ ረዓብን እና ቤተሰቧቿን ከከተማይቱ ያወጡትን ሁለት ወጣት ወንዶች ብቻ የሚያመለክት አይደለም፡፡

Joshua 6:25

እርሷ በእስራኤል ውስጥ ትኖራለች

"እርሷ" የሚለው ቃል ረዓብን እና ትውልዷቿን ያመለክታል፡፡ "የእርሷ ትውልድ በእስራኤል ይኖራል" (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ ዛሬ ድረስ

"አሁን" ወይም "ዛሬ ድረስ፡፡" የመጀመሪያው ጸሐፊ ይህንን ታሪክ እንደጻፈው የረዓብ ትውልዶች አሁንም በእስራኤል ይኖራሉ

Joshua 6:26

ዳግም የሚገነባት ሰው በያህዌ ዐይኖች ፊት የተረገመ ነው

በያህዌ አይኖች ፊት የተረገመ የሚለው የሚገልጸው በያህዌ የተረገመ ማለትን ነው፡፡ "ዳግም የሚገነባት ሰው ያህዌ የረገመው ይሁን" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

መሰረቱን የሚጥለው/ የሚመሰርተው በመጀመሪያ ልጁ የህይወት ዋጋ ይሁን/መሰረቱን ሲጥል የበኩር ልጁ ይሙት

ለኢያሪኮ አዲስ መሰረትን የሚጀምር ሰው የሚከፍለው ዋጋ የመጀመሪያ ልጁ መሞት ነው፡፡ ይህ የተነገረው ሰውየው ለስራው እንደሚከፍለው ተመን/ዋጋ ተደርጎ ነው፡፡ "መሰረቱን ከጣለ፣ የመጀመሪያ ወንድ ልጁን ያጣል" ወይም "መሰረቱን ከጣለ፣ የመጀመሪያ ልጁ ይሞታል" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በታናሹ ልጁ የህይወት ዋጋ በሮቿን ያቆማል/በሮቿን ሲያቆም ታናሹ ልጁ ይሙት

የኢያሪኮን አዲስ በሮች የሚያቆም ሰው የሚከፍለው ዋጋ የታኛሹ ልጁ መሞት ነው፡፡ ይህ የተነገረው ሰውየው ለስራው እንደሚከፍለው ተመን/ዋጋ ተደርጎ ነው፡፡ "በሮቿን ካቆመ፣ የመጨረሻ ልጁን ያጣል" ወይም " "በሮቿን ካቆመ፣ የመጨረሻ ልጁ ይሞታል" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ዝናው በምድሪቱ ሁሉ ተስፋፋ

ይህ የያህዌን ሳይሆን፣ የኢያሱን ዝና ያመለክታል፡፡ በምድሪቱ በሚኖሩ መሃል ታዋቂ ሆነ የሚለው የተገለጸው ዝናው እንደተስፋፋ ተደርጎ ነው፡፡ "ኢያሱ በምድሪቱ ሁሉ ዝነኛ ሆነ" ወይም "በምድሪቱ የሚኖሩ ሰዎች ስለ ኢያሱ አወቁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 7

1 የእስራኤል ሕዝብ ግን እንዲጠፉ ከተለዩ ነገሮች በመውሰድ ታማኝነትን አጎደሉ። ከይሁዳ ነገድ የሆነ አካን፥ እርሱም የከርሚ ልጅ፥ የዘንበሪ ልጅ፥ የዛራ ልጅ፥ እንዲጠፉ ከተለዩት ነገሮች ወስደ፤ የእግዚአብሔርም ቁጣ በእስራኤል ሕዝብ ላይ ነደደ። 2 ኢያሱም ከቤቴል በምሥራቅ በኩል በቤት አዌን አጠገብ ወዳለችው ወደ ጋይ ከኢያሪኮ ሰዎችን ላከ። እርሱም፦ ውጡ ምድሪቱንም ሰልሉ ብሎ ተናገራቸው። ሰዎቹም ወጡ፥ ጋይንም ሰለሉ። 3 እነርሱም ወደ ኢያሱ ተመልሰው፡- ሕዝብን ሁሉ ወደ ጋይ አትላክ። ጋይን እንዲመቱ ሁለት ወይም ሦስት ሺህ ያህል ሰዎች ብቻ ይላክ። የጋይ ሰዎች በቁጥር ጥቂቶች ስለሆኑ ሕዝብ ሁሉ በውጊያ እንዲደክም አታድርግ። 4 ከሠራዊቱ ሦስት ሺህ ያህል ሰዎች ብቻ ወደዚያ ወጡ፤ እነርሱም ከጋይ ሰዎች ፊት ሸሹ። 5 የጋይም ሰዎች ከእነርሱ ሠላሳ ስድስት ያህል ሰዎችን መቱ፥ ከበሩ እስከ ሸባሪም ድረስ አባረሩአቸው፤ በቁልቁለቱም መቱአቸው። የሕዝቡም ልብ ፈራ፤ ድፍረትንም አጡ። 6 ኢያሱም ልብሱን ቀደደ። እርሱና የእስራኤልም ሽማግሌዎች በእግዚአብሔር ታቦት ፊት እስከ ማታ ድርስ በግምባራቸው ተደፉ፤ በራሳቸውም ላይ ትቢያ ነሰነሱ። 7 ኢያሱም አለ፦ ወዮ ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፦ ይህን ሕዝብ ቀድሞኑ ዮርዳኖስን ለምን አሻገርኸው? እንዲያጠፉን በአሞራውያን እጅ ለምን አሳልፈህ ሰጠሃን? ከዚህ የተለየ ምርጫ ማድረግ በቻልንና በዮርዳኖስም ማዶ በተመቀመጥን ይሻለን ነበር። 8 ጌታ ሆይ የእስራኤል ሕዝብ በጠላቶቻቸው ፊት ከሸሹ በኋላ ምን ማለት እችላለሁ? 9 ይህንን ከነዓናውያንና በምድሪቱም የሚኖሩ ሁሉ ይሰማሉ። እነርሱም ይከብቡናል፥ በምድር ያሉትም ሕዝብ ስማችን እንዲረሳ ያደርጋሉ። ለታላቁ ስምህስ የምታደርገው ምንድን ነው? 10 እግዚአብሔርም ኢያሱን አለው፦ተነስተህ ቁም! ለምን በግምባርህ ተደፍተሃል? 11 እስራኤል ኃጢአትን አድርጎአል። ያዘዝኋቸውንም ቃል ኪዳኔን አፍርሰዋል። ለጥፋት ከተለዩት ነገሮችን ሰርቀዋል፤ ሰርቀው የወሰዱትንም ኃጢአት በዕቃቸውም ውስጥ ሸሸጉት። 12 በዚህም ምክንያት የእስራኤል ሕዝብ በጠላቶቻቸው ፊት መቆም አይችሉም። ራሳቸው ለጥፋት የተለዩ ሆነው በጠላቶቻቸው ፊት ሸሹ። በመካከላችሁ እስካሁን ያለውን መወገድ ያለበትን እርም ከመካከላችሁ ካላጠፋችሁ ከዚህ በኃላ ከእናንተ ጋር አልሆንም። 13 ተነሣና ሕዝቡን ቀድስልኝ፤ እንዲህም በላቸው፦ራሳችሁን ለነገ ለእግዚአብሔር ቀድሱ ይላል የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር፤ እስራኤል ሆይ ፥ሊጠፉ የሚገቡ ነገሮች እስካሁን በመካከላችሁ አለ። መጥፋት ያልባቸው ነገሮች ከመካከላችሁ እስክታጠፉ ድረስ በጠላቶቻችሁ ፊት መቆም አትችሉም። 14 ነገም ራሳችሁን በየነገዳችሁ ታቀርባላችሁ፤ እግዚአብሔርም በዕጣ የሚለየው ነገድ በየወገኖቹ ይቀርባል። እግዚአብሔርም የሚለየው ወገን በየቤተ ሰቦቹ ይቀርባል። እግዚአብሔርም የሚለየው ቤተ ሰብ አንድ በአንድ ይቀርባል። 15 ለጥፋትም የተለየ ነገር የተገኘበት ሰው የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን በማፍረሱና በእስራኤልም ላይ ክፉ ነገር እንዲመጣ በማድረጉ እርሱና ለእርሱም ያለው ነገር ሁሉ በእሳት ይቃጠላል። 16 ኢያሱም ማልዶ ተነሣ፥ እስራኤልንም በየነገዶቻቸው አቀረበ፤ የይሁዳም ነገድ ተለየ። 17 የይሁዳንም ወገን አቀረበ፥የዛራም ወገን ለየ። የዛራንም ወገን እያንዳንዱን አቀረበ፤ ዘንበሪም ተለየ። 18 የቤተ ሰቡንም እያንዳንዱን አቀረበ፤ ከይሁዳም ነገድ የሆነ የከርሚ ልጅ የዘንበሪ ልጅ የዛራ ልጅ አካን ተለየ። 19 ከዚያ ኢያሱ አካንን አለው፦ ልጄ ሆይ፥ በእስራኤልም አምላክ ፊት እውነቱን ተናገር፥ ለእርሱም ተናዘዝ። ያደረግኸውንም ንገረኝ፤ ከእኔም አትሸሽግ። 20 አካንም መልሶ ኢያሱን እንዲህ አለ፦ በእውነት የእስራኤልን አምላክ እግዚአብሔርን በድያለሁ። ያደረግሁትም ይህንን ነው፦ 21 በዘረፋ መካከል አንድ የሚያምር የባቢሎን ኮት፥ ሁለት መቶም ሰቅል ብር፥ ሚዛኑም አምሳ ሰቅል የሆነ ወርቅ አይቼ ተመኘኋቸው፥ ወሰድኋቸውም። እነሆም፥ በድንኳኔ ውስጥ በመሬት ተሸሽገዋል፥ ብሩም ከሁሉ በታች ነው አለው። 22 ኢያሱም መልእክተኞችን ሰደደ፥ ወደ ድንኳኑም ሮጡ፤ ዕቃዎቹም ነበሩ። በድንኳኑም ውስጥ ተሸሽጎ አገኙት ብሩም ከበታች ነበረ። 23 ከድንኳኑም መካከል ዕቃዎቹን ወስደው ወደ ኢያሱና ወደ እስራኤል ሕዝብ ሁሉ አመጡት። በእግዚአብሔርም ፊት አኖሩት። 24 ኢያሱና እስራኤል ሁሉ የዛራን ልጅ አካንን፥ ብሩንም፥ ኮቱንም፥ ወርቁንም፥ ወንዶችንና ሴቶች ልጆቹንም፥ በሬዎቹንም፥ አህያውዎቹንም፥ በጎቹንም፥ ድንኳኑንም፥ ያለውንም ሁሉ ወስደው ወደ አኮር ሸለቆ አመጡአቸው። 25 ኢያሱም እንዲህ አለው፦ ለምን አስጨነቅኸን? እግዚአብሔርም ዛሬ ያስጨንቅሃል። እስራኤልም ሁሉ በድንጋይ ወገሩት፤ሁሉንም በእሳትም አቃጠሉአቸው፥ በድንጋይም ወገሩአቸው። 26 በላዩም እስከ ዛሬ ድረስ ያለ ታላቅ የድንጋይ ክምር ሆነ። እግዚአብሔርም ከቁጣው ትኩሳት ተመለሰ። ስለዚህም የዚያ ስፍራ ስም እስከ ዛሬ ድረስ የአኮር ሸለቆ ነው።



Joshua 7:1

ለመደምሰስ/መጥፋት የተለዩ ነገሮች

"ያህዌ ፈጽማችሁ በማጥፋት/በመደምሰስ ለእኔ ለዩልኝ ያላቸው ነገሮች"

አካን…ከርሚ…ዘንበሪ…ዛራ

እነዚህ የወንድ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የያህዌ ቁጣ ነደደ

"ቁጣ" እና "ነደደ" የሚሉት የሚገልጹት በአካል እሳት እንዳለ ሳይሆን የቁጣውን ከፍተኛነት ደረጃ ነው፡፡ "የያህዌ ቁጣ እንድ እሳት ነደደ" ወይም "ያህዌ እጅግ ተቆጥቶ ነበር" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 7:2

ህዝቡ ሁሉ

ይህ የሚያመለክተው የእስራኤልን ሰራዊት ነው፡፡

እነርሱ በቁጥር ጥቂት ናቸው

"እነርሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው የጋይን ሰዎች ነው፡፡

Joshua 7:4

ከሰራዊቱ ሶስት ሺህ ወንዶች ተነስተው ወጡ

እነዚህ ወንዶች የሰራዊቱ ክፍል ነበሩ፡፡ "የሰራዊቱ ክፍል የሆኑ ሶስት ሺህ ወንዶች ወጡ"

ሶስት ሺህ ወንዶች…ሰላሳ ስድስት ወንዶች

"3,000 ወንዶች… 36 ወንዶች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የህዝቡ ልብ ቀለጦ እንደ ውሃ ሆነ

"ቀለጠ" እና "እንደ ውሃ ሆነ" የሚሉት ሃረጋት ተመሳሳይ ትርጉምን ይጋራሉ፤ በአንድነት ተቀናጅተው የቀረቡት ሰዎቹ እጅግ ፈርተው እንደነበር አጉልቶ ለማሳየት ነው፡፡ (ትይዩ ንጽጽዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

የህዝቡ ልብ ቀለጠ

እዚህ ስፍራ ላይ ህዝቡ የተገለጸው በእነርሱ "ልቦች" ነው ይህም ስሜቶቻቸውን በትኩረት ለመግለጽ ነው፡፡ "ህዝቡ እጅግ ፈርቶ ነበር" (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ ሚለውን ይመልከቱ

የህዝቡ ልብ

"ህዝቡ" የሚለው ሃረግ የሚያመለክተው እስራኤላውያን ወታደሮችን ነው፡፡

Joshua 7:6

ልብሶቹን ቀደደ… በጭንቅላታቸው አብዋራ ነስንሰው በያህዌ ታቦት ፊት በግንባራቸው ተደፉ

እነዚህን ነገሮች ያደረጉት በእግዚአብሔር ፊት ምን ያህል እንዳዘኑ እና እንደተጨነቁ ለማሳየት ነው፡፡ (ትዕምርታዊ/ምልክታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

ያጠፉን ዘንድ ለአሞራውያን እጆች አሳልፈህ ልትሰጠን ነውን?

ኢያሱ እግዚአብሔር ዮርዳኖስን አሻግሮ ያመጣቸው ምክንያቱ ይህ እንደሆነ እየጠየቀ ነበር፡፡ "ይህን የደረግከው አሞራውያን ያጠፉን ዘንድ ለእነርሱ እጆች አሳልፈህ ልትሰጠን ነውን?" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ኢሊፕሰስ/የተተወ የሚለውን ይመልከቱ)

ያጠፉን ዘንድ ለአሞራውያን እጆች አሳልፈህ ልትሰጠን ነውን?

የአሞራውያን እጆች የሚለው የሚገልጸው አቅማቸውን እና ሃይላቸውን ነው፡፡ እነርሱን ለመደምሰስ እስራኤላውያንን ለእጆቻቸው መስጠት የሚለው የሚገልጸው አሞራውያን እስራኤላውያንን እንዲቆጣጠሩ እና እንዲያጠፏቸው መፍቀድን ነው፡፡ "አሞራውያን እንዲያጠፉን ትፈቅዳለህን?" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ምነው ሌላ ውሳኔ ባደረግን ኖሮ

"ባደረግን ኖሮ" የሚለው ቃል የሚያሳየው አንድ ነገር ምነው ባልሆነ ኖሮ የሚል ፍላጎትን መግለጫ ነው፡፡ "ምነው የተለየ ውሳኔ አድርገን ቢሆን ኖሮ"

Joshua 7:8

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ መጨነቁን ለያህዌ ይገልጻል

እስራኤል ጀርባውን ለጠላቶቹ ከሰጠ በኋላ ምን ማለት እችላለሁ?

ኢያሱ ይህን የሚናገረው ምን መናገር እንዳለበት እንኳን እስከሚረበሽ ድረስ ተስፋ መቁረጡን ለመግለጽ ነው፡፡ "ምን ማለት እንዳለብኝ አላውቅም፡፡ እስራኤል ጀርባውን ለጠላት ሰጥቷል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

እስራኤላውያን ጀርባቸውን በጠላቶቻቸው ፊት አዙረዋል

ይህንን ማድረግ የሚገልጸው ከጠላቶቻቸው ፊት መሸሻቸውን ነው፡፡ "እስራኤል ከጠላቶቻቸው ሸሽተዋል/ እስራኤላውያንን ጠላቶቻቸው አሳደዋቸል" (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱ እኛን ይከባሉ፣ ደግሞም በምድር የሚኖሩ ሰዎች ስማችንን እንዲረሱ ያደርጋሉ

ሰዎች የእስራኤልን ስም እንዲረሱ ማድረግ የሚገልጸው፤ እስራኤላውያንን እንዲረሱ ማድረግን ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ይህንን የሚያደርጉት እስራኤላውያንን በመግደል ነው፡፡ "ይከቡናል፣ ይገድሉንማል፤ ደግሞም የምድር ህዝብ ሁሉ ይረሳናል፡፡" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት እና ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚሉትን ይመልከቱ)

ለታላቁ ስምህ

"ታላቁ ስምህ" የሚለው ሃረግ እዚህ ስፍራ የሚገልጸው የእግዚአብሔርን ዝና እና ሃይል ነው፡፡ "እናም ስለዚህ አንተ ታላቅ መሆንህን ህዝቦች ያውቁ ዘንድ ምን ታደርጋለህ" (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ለታላቁ ስምህ ምን ታደርጋለህ?

ኢያሱ ይህንን ጥያቄ ያነሳው እስራኤላውያን ከተደመሰሱ፣ ሌሎች ህዝቦች እግዚአብሔር ታላቅ አይደለም ብለው ያስባሉ የሚለውን ለእግዚአብሔር ለማሳሰብ/ እግዚአብሔርን ለማስጠንቀቅ ነው፡፡ "ከዚያ ለስምህ ታላቅነት ልታደርገው የምትችለው ምንም ነገር አይኖርም" ወይም "ከዚያ ሰዎች አንተ ታላቅ መሆንህን አያውቁም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ እና ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 7:10

አጠቃላይ መረጃ፡

ያህዌ እስራኤል ለምን እንደተረገመ ለኢያሱ መለሰለት፡፡

ለምን በዚያ በፊትህ ተደፋህ?

እግዚአብሔር ይህንን ጥያቄ የተጠቀመበት ኢያሱ በዚያ በፊቱ መደፋቱን ለመገሰጽ ነው፡፡ "በአፍር ላይ በዚያ መደፋትህን አቁም!" (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ)

ተለይተው ተቀምጠው የነበሩት ነገሮች

እነዚህ በኢያሱ 6፡18-19 "እንዲጠፉ የተለዩ" ነገሮች ናቸው፡፡ "የተረገሙት ነገሮች" ወይም "እግዚአብሔር የረገማቸው ነገሮች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡

ሰርቀዋል ከዚያም ደግሞ ኃጢአታቸውን ደብቀዋል

ኃጢአታቸውን መደበቅ የሚለው የሚገልጸው ኃጢአት መስራታቸውን ሌሎች እንዳያውቁ ለማድረግ መሞከራቸውን ይገልጻል፡፡ "እነዚያን ነገሮች ሰርቀዋል፣ ከዚያም ቀጥሎ ኃጢአት መስራታቸውን ሰዎች እንዳያውቁ ለማድረግ ሞክረዋል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በጠላቶቻቸው ፊት መቆም አይችሉም

በጠላቶቻቸው ፊት መቆም የሚለው የሚወክለው ጠላቶቻቸውን ውጤታማ ሆነው መውጋት አይችሉም የሚለውን ነው፡፡ "ጠላቶቻቸውን ውጤታማ ሆነው መውጋት አይችሉም" ወይም "ጠላቶቻቸውን ማሸነፍ አይችሉም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ለጠላቶቻቸው ጀርባቸውን አዞሩ/ጀርባቸውን አዙረው ሸሹ

ይህንን ማድረግ የሚወክለው ከጠላቶቻቸው መሸሻቸውን ነው፡፡ "ከጠላቶቻቸው ሸሹ" (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ከእንግዲህ ከእናንተ ጋር አልሆንም

ከእስራኤል ጋር መሆን የሚወክለው እስራኤልን መርዳትን ነው፡፡ "ከእንግደህ በኋላ አልረዳችሁም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 7:13

አያያዥ ሃሳብ፡

ያህዌ ከኢያሱ ጋር መነጋገሩን ቀጠለ፤ ደግሞም ለህዝቡ መናገር ያለበትን ነገረው፡፡(ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ህዝቡ

ይህ የእስራኤልን ህዝብ ያመለክታል

ጠላቶቻችሁን መቋቋም አትችሉም

ከጠላቶቻቸው ፊት መቆም የሚገልጸው ከጠላቶቻቸው ጋር ተዋግተው በስኬት ማሸነፍን ነው፡፡ "ከጠላቶቻችሁ ጋር በስኬት መዋጋት አትችሉም" ወይም "ጠላቶቻችሁን ማሸነፍ አትችሉም"

Joshua 7:14

አያያዥ ሃሳብ፡

ያህዌ ከኢያሱ ጋር መነጋገሩን ቀጠለ፤ ደግሞም ለህዝቡ መናገር ያለበትን ነገረው፡፡

ራሳችሁን በየነገዳችሁ ማቅረብ አለባችሁ

የእስራኤልን ህዝብ የሚመሰርቱ አስራ ሁለት ነገዶች ነበሩ፡፡ "በየነገዶቻችሁ" የሚለው ሃረግ ትርጉሙ "በእያንዳንዱ ነገድ" ማለት ነው፡፡ "እያንዳንዳቸው ነገዶቻችሁ ራሳቸውን ለያህዌ ማቅረብ ይኖርባቸዋል " በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ያህዌ የሚለየው ነገድ በየጎሳው ይቀርባል

ነገድ ከበርካታ ጎሳ የሚመሰረት ነው፡፡ "ያህዌ ከለየው ነገድ፣ እያንዳንዱ ጎሳ ወደፊት ይቀርባል" (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ያህዌ የሚለየው ነገድ

የእስራኤል መሪዎች እጣ ያወጣሉ፣ እናም ይህንን በማድረግ፣ ያህዌ የለየውን ነገድ ያውቃሉ፡፡ ይህ ይበልጥ በግልጽ ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ያህዌ በእጣ የሚለየው ነገድ" ወይም "እጣ ስናወጣ ያህዌ የሚለየው ነገድ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡

ያህዌ የሚለየው ጎሳ በእያንዳንዱ ቤተሰብ መቅረብ ይኖርበታል

ጎሳ በብዙ ቤተሰቦች የሚመሰረት ነበር፡፡ "ያህዌ ከሚለየው ጎሳ፣ እያንዳንዱ ቤተሰብ ወደፊት መቅረብ ይኖርበታል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ያህዌ የሚለየው ቤተሰብ በነፍስ ወከፍ መቅረብ ይኖርበታል

ቤተሰብ በርካታ ሰዎች በውስጡ ነበሩት፡፡ "ያህዌ ከለየው ቤተሰብ፣ እያንዳንዱ ሰው ወደፊት መቅረብ ይኖርበታል" (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የተለየው ሰው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ያህዌ የለየው ሰው" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

እርሱ የያህዌን ቃልኪዳን አፍርሷል

ቃልኪዳንን ማፍረስ የሚለው ያለመታዘዝን ያመለክታል፡፡ "እርሱ የያህዌን ቃል ኪዳን አፍርሷል" (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 7:16

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ እስራኤልን በያህዌ ፊት ለማቅረብ የያህዌን ትዕዛዝ ተከተለ

እስራኤልን በየነገዱ ወደፊት አቀረበ

"በየነገዱ/ነገድ በነገድ" የሚለው ሃረግ እያንዳንዱ ነገድ ማለት ነው፡፡ "እያንዳንዱን የእስራኤል ነገድ ወደፊት አቀረበ" (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የይሁዳ ነገድ ተለየ

ይህ በዐድራጊ አረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ያህዌ የይሁዳን ነገድ ለየ" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ፡፡

የዛራውያንን ጎሳ በነፍስ ወከፍ አቀረበ

"በነፍስ ወከፍ/ በግለሰብ" የሚለው ሃረግ እያንዳንዱ ሰው የሚል ትርጉም የሚሰጥ ፈሊጥ ነው፡፡ በዚህ ዐረፍተ ነገር ውስጥ ግለሰቦች የተባሉት የቤተሰባቸው መሪዎች/አባወራ ነበሩ፡፡ "እርሱም የዛራውያንን ጎሳዎች እያንዳንዱን ሰው ወደፊት አቀረበ" ወይም "ከዛራውያን ጎሳ የቤተሰቡ መሪ የሆን እያንዳንዱን ሰው ወደፊት አቀረበ" (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚሉትን ይመልከቱ)

የዛራውያን ጎሳ

ጎሳው ስሙን ያገኘው ዛራ ከተባለው ሰው ስም በመነሳት ነው

ዘንበሪ…አካን…ከርሚ…ዛራ

እነዚህ የወንዶች ስሞች ናቸው፡፡ እነዚህን በኢያሱ 7፡1 ላይ በተረጎሙበት መሰረት ይተርጉሙ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 7:19

ለእርሱ ኑዛዜያችሁን/ንስሃ አቅርቡ

"ንስሃ/ኑዛዜ" የሚለው ረቂቅ ስም "ተናዘዘ" በሚል ግስ ሊገለጽ ይችላል፡፡ "ለእርሱ ተናዘዝ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ረቂቅ ስሞች የሚለውን ይመልከቱ)

ነገሩን ከእኔ አትደብቅ

መረጃን መደበቅ የሚወክለው አንድ ሰው ነገሩን እንዳያውቅ ጠብቆ ለመያዝ መሞከርን ነው፡፡ "ያደረግከውን እንዳላውቅ ልትሸሽገኝ አትሞክር" (ዘይቤያዊ አነጋገርየሚለውን ይመልከቱ)

ሁለት መቶ ሰቅል

ይህ ከሁለት ኪሎ ግራም በላይ ነው፡፡(መጽሐፍ ቅዱሳዊ የክብደት መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

ሃምሳ ሰቅል

ይህ ከ500 ግራም በላይ ነው፡፡ (መጽሐፍ ቅዱሳዊ የክብደት መለኪያ የሚለውን ይመልከቱ)

በመሬት ውስጥ ተደብቀዋል

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "እኔ በመሬት ውስጥ ደብቄያቸዋለሁ" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 7:22

እነርሱ አዩ/አገኙ

"ኢያሱ የላካቸው ሰዎች አዩ/አገኙ"

እቃዎቹን አውጥተው ዘረገፉ

በእርስዎ ቋንቋ ውስጥ የሚገኝን በርካታ ትንንሽ እቃዎችን ከትልቅ ቦርሳ/ሻንጣ መሬት ላይ መድፋትን የሚገልጽ ቃል ይጠቀሙ

Joshua 7:24

የአኮር ሸለቆ

የስሙ ትርጉም "የችግር ሸለቆ" ማለት ነው፣ ነገር ግን አኮርን በተጻፈበት አጠራሩ እንዳለ አኮር ብሎ መተርጎሙ ይመረጣል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 7:25

ለምን አስጨነቅከን?

ኢያሱ ይህንን ጥያቄ የተጠቀመበት አካንን ለመገሰጽ ነው፡፡ "አንተ አኛን አስጨነቅከን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሰሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ከዚይም የቀሩትን በድንጋይ ወገሯቸው፤ ደግሞም በእሳት አቃጠሏቸው፡፡

ሊሰጡ የሚችሉ አማራጭ ትርጉሞች 1)እስራኤላውያን የአካንን ቤተሰብ አቃጥለው ገደሉ፤ከዚያም ድንጋይ ከመሩባቸው ወይም 2) እስራኤላውያን የአካንን ቤተሰብ በድንጋይ ወግረው ገደሉ ከዚያም በድናቸውን አቃጠሉ ወይም 3) አካን እና ያለው ሁሉ በድንጋይ ተወገረ ከዚያም ተቃጠለ

ያህዌ የነድ ቁጣውን አራቀ

ቁጣውን አራቀ የሚለው የሚገልጸው ቁጣውን አቆመ ማለት ነው፡፡ የሚነድ ቁጣ የሚለው የሚወክለው ጠንካራ ቁጣን ነው፡፡ "ያህዌ ከቁጣው ተመለሰ/መቆጣቱን አቆመ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ ዛሬ ድረስ

ጸሐፊው ይህንን እስከጻፈበት ጊዜ ድረስ የአኮር ሸለቆ ተብሎ ይጠራ ነበር


Chapter 8

1 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ አለ፦ አትፍራ አትደንግጥ። ጦረኞችንም ሁሉ ከአንተ ጋር ውሰድ ተነሥተህም ወደ ጋይ ውጣ። ተመልከት፥ የጋይን ንጉሥ፥ ሕዝቡን፥ ከተማውንና ምድሩን በእጅህ ሰጥቼሃለሁ። 2 በኢያሪኮና በንጉሥዋም እንዳደረግህ እንዲሁ በጋይና በንጉሥዋ ታደርጋለህ፤ ምርኮውንና ከብቱን ግን ለራሳችሁ ትወስዳላችሁ። ከከተማይቱም በስተ ኋላ ድብቅ ጦር አዘጋዝጅ አለው። 3 ኢያሱም ተነሣና ጦረኞቹንም ሁሉ ወደ ጋይ ወሰዳቸው። ኢያሱም ጽኑዓን ኃያላን የሆኑትን ሠላሳ ሺህ ሰዎች መርጦ በሌሊትም ሰደዳቸው። 4 እንዲህም ብሎ አዘዘቸው፦ እነሆ፥ከከተማይቱ በስተ ኋላ ተደበቁ። ከከተማይቱ በጣም ርቃችሁ አትሂዱ፤ነገር ግን ሁላችሁም ተዘጋጁ። 5 እኔና ከእኔም ጋር ያለው ሕዝብ ሁሉ ወደ ከተማይቱ እንቀርባለን። እንደ በፊቱ ሊያጠቁን በሚመጡበት ጊዜ ከፊታቸው እንሸሻለን። 6 አስቀድመን እንደ ሸሸን፥ የምንሸሸ ይመስላቸዋል፥ ከከተማይቱ እስክናርቃቸው ድረስ ወጥተው ይከተሉናል። እንዲህም ይላሉ፦ባለፈው እንዳደረጉት ከፊታችን እየሸሹ ነው። እኛም ከእነርሱ እንሸሻለን። 7 እናንተም ከተደበቃችሁበት ስፍራ መጥታችሁ ከተማዋን ትይዛላችሁ። እግዚአብሔር አምላካችሁም እርስዋን በእጃችሁ አሳልፎ ይሰጣችኋል። 8 ከተማይቱንም በያዛችኋት ጊዜ በእሳት አቃጥሉአት። በእግዚአብሔርም ቃል እንደታዘዛሁ ታደርጋላችሁ። እነሆ፥ አዝዣችኋለሁ። 9 ኢያሱም ሰደዳቸው፤ እነርሱም ወደሚደበቁበት ስፍራ ሄደው፥ በጋይና በቤቴል መካከልም ከጋይ በስተምዕራብ ተደበቁ። ኢያሱ ግን በዚያች ሌሊት በሕዝቡ መካከል አደረ። 10 ኢያሱም ማልዶ ተነሣና ሕዝቡን አሰለፈ፤እርሱና የእስራኤልም ሽማግሌዎች የጋይን ሕዝብ አጠቁ ። 11 ከእርሱም ጋር የነበሩ ጦረኞች ሁሉ ሄደው፥ ወደ ከተማይቱ ደረሱ። ወደ ከተማይቱ አጠገብ መጡና በሰሜን በኩል በጋይ ሰፈሩ። በእነርሱና በጋይ መካከል ሸለቆ ነበረ። 12 አምስት ሺህ ያህል ሰዎችንም ወስዶ በቤቴልና በጋይ መካከል በከተማይቱም በምዕራብ በኩል በድብቅ አስቀመጣቸው። 13 በከተማይቱ የነበሩትን ሠራዊት ሁሉ፤ በከተማይቱ ሰሜን በኩል ዋና ጦርና በከተማይቱ ምዕራብ በኩል ደጀን ጦር ጠባቂዎችን አኖሩ። ኢያሱም በዚያች ሌሊት በሸለቆው አደረ። 14 የጋይም ንጉሥ ባየ ጊዜ ይህ ስለታወቀ፥እርሱና ሠራዊቱ በማለዳ ተነስተው እስራኤልን ለማጥቃት ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ሸለቆ ወዳለው ሰፍራ ቸኮሉ። ከከተማይቱ በስተ ኋላ ግን ድብቅ ጦር ለማጥቃት እንዳለ አያውቅም ነበር። 15 ኢያሱና እስራኤል ሁሉ ራሳቸው በፊታቸው ድል የተነሡ መስለው ወደ ምድረ በዳው መንገድ ሸሹ። 16 በከተማይቱም የነበሩ ሰዎች ሁሉ በአንድነት ከኋላቸው እንዲሄዱ ተጠሩ፤ ኢያሱንም አሳደዱት፥ ከከተማይቱም ርቀው ወጡ። 17 በጋይና በቤቴልም ውስጥ እስራኤልን ለማሳደድ ያልወጣ ሰው አልነበረም። ከተማይቱንም ክፍት አድርገው፥ እስራኤልን አሳደዱ። 18 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ አለ፦ በእጅህ ያለውን ጦር በጋይ አነጣጥር፤ ጋይንም በእጅህ አሳልፌ እሰጥሃለሁ። ኢያሱም በእጁ ያለውን ጦር በከተማይቱ ላይ ዘረጋ። 19 የተደበቁትም ሠራዊት ፈጥነው ከስፍራቸው ወጥተው ኢያሱም እጁን እንደ ዘረጋ ሮጡ። ወደ ከተማይቱም ሮጡ፤ ገብተውም ያዙአት። ፈጥነውም ከተማይቱን በእሳት አቃጠሉአት። 20 የጋይም ሰዎች ወደ ኋላቸው ዞረው ተመለከቱ። ከከተማይቱ ወደ ሰማይ የሚወጣውን ጢስ አዩ፤ ወዲህ ወይም ወዲያም መንገድ ማምለጥ አልቻሉም። ወደ ምድረ በዳ ሸሽተው የነበሩ የእስራኤላውያን ጦር ሠራዊት ያሳድዱአቸው የነበሩትን ለመግጠም ተመለሱ። 21 ኢያሱና እስራኤል ሁሉ ድብቅ ጦር ከተማይቱን እንደ ያዙ ወደ ላይ ከሚወጣ ጢስ ጋር ባዩ ጊዜ፥ ወደ ኋላ ተመልሰው የጋይን ሰዎች ገደሉ። 22 ሌሎቹም ወደ ከተማይቱ ሄደው የነበሩ የእስራኤል ሠራዊት ለማጥቃት ወጡ። ስለዚህም የጋይ ሰዎች በእስራኤል ሠራዊት መካከል ሌሎቹ በዚህ በኩልና ሌሎቹ በዚያ በኩል ተያዙ። እስራኤልም የጋይን ሰዎች አጠቁአቸው፤ አንዳቸውም አልተረፉም፤ አላመለጡምም። 23 በሕይወት የያዙትን የጋይንም ንጉሥ ማርከው ወደ ኢያሱ አመጡት። 24 እንዲህም ሆነ፤ የጋይን ሰዎች ሁሉ በሜዳና በምድረ በዳ አጠገብ እስራኤልን ሲያሳድዱ በነበሩበት ቦታ ሁሉም የመጨረሻ በሰይፍ ስለት እስኪ ወድቁ ድረስ ጨርሰው ከገደሉአቸው በኋላ፥ እስራኤል ሁሉ ወደ ጋይ ተመለሱ። በሰይፍም ስለት መቱአቸው። 25 በዚያም ቀን በሰይፍ ስለት የወደቁት ወንዶችና ሴቶች የጋይ ሰዎች ሁሉ አሥራ ሁለት ሺህ ነበሩ። 26 ኢያሱም የጋይን ሰዎች ሁሉ ፈጽሞ እስኪያጠፋ ድረስ ጦር የዘረጋባትን እጁን አላጠፈም። 27 እስራኤላውያንም እግዚአብሔር ኢያሱን እንዳዘዘው የዚያችን ከተማ ከብትና ምርኮ ለራሳቸው ወሰዱ። 28 ኢያሱም ጋይን አቃጠላት፥ ለዘላለም የፍርስራሽ ክምር እንዲሆን አደረጋት። እስከ ዛሬም ድረስ ባዶ ስፍራ ሆነች። 29 የጋይንም ንጉሥ እስከ ማታ ድረስ በዛፍ ላይ ሰቀለው። ኢያሱም ፀሐይ በገባች ጊዜ የንጉሡን አስክሬን ከዛፍ አወርደው፥ በከተማይቱ በር አደባባይ እንዲጥሉት አዘዘ። በላዩም ታላቅ የድንጋይ ክምር አደረጉት። እስከ ዛሬ ድረስም ይህ የድንጋይ ክምር አለ። 30 ከዚያም ኢያሱ በጌበል ተራራ ላይ ለእስራኤል አምላክ ለእግዚአብሔር መሠዊያን ሠራ። 31 የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ እንዳዘዘ፦ በሙሴም ሕግ መጽሐፍ እንደተጻፈው፥ መሠዊያው ካልተወቀረ ድንጋይና ብረት ካልነካው ነበረ። በእርሱም ላይ ለእግዚአብሔር የሚቃጠለውን መሥዋዕት አቀረቡ፥ የደኅንነትንም መሥዋዕት ሠዉ። 32 የእስራኤልም ሰዎች ፊት በድንጋዮቹ ላይ የሙሴን ሕግ ቅጂ ጻፈባቸው። 33 እስራኤል ሁሉ፥ ሽማግሌዎቻቸውም፥ አለቆቻቸውም፥ ፈራጆቻቸውም፥ በመጻተኞችና በአገሩ ልጆች ፥እኩሌቶቹ በገሪዛን ተራራ ፊት ለፊት እኩሌቶቹም በጌባል ተራራ ፊት ሆነው የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን ታቦት በተሸከሙት በካህናትና በሌዋውያን ፊት ለፊት፥ በታቦቱም ፊት በወዲህና በወዲያ ቆመው ነበር። የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ እንዳዘዘ፥የእስራኤልን ሕዝብ አስቀድሞ ባረኩ። 34 ከዚህም በኋላ ኢያሱ በሕጉ መጽሐፍ እንደ ተጻፉ የሕጉን ቃሎች ሁሉ በረከቱንና እርግማኑን አነበብ። 35 ኢያሱም በእስራኤል ጉባኤ ሁሉ ፊት በሴቶቹም፥ በሕፃናቱም፥ በመካከላቸውም በሚኖሩት መጻተኞች ፊት ሙሴ ካዘዘው አንዲት ቃል ሳያስቀር ሁሉን አነበበ ።



Joshua 8:1

አትፍሩ፣ ተስፋ አትቁረጡ

እነዚህ ሁለት ሃረጋት በመሰረቱ ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፡፡ ያህዌ ያቀናጃቸው ለፍርሃት አንዳች ምክንያት ስለሌለ ነው፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

የጋይን ንጉሥ… እና ምድሩን በእጆችህ አሳልፌ ሰጥቼሃለሁ

እነርሱን ለእስራኤላውያን እጆች አሳልፎ መስጠት የሚወክለው ለእስራኤል ድልን እና የበላይነትን መስጠትን ነው፡፡ "በጋይ ንጉሥ እና በህዝቡ ላይ ደግሞም በእርሱ ከተማ እና በምድሩ ላይ ድልን ሰጥቼሃለሁ" (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

እኔ ሰጥቼሃለሁ

እግዚአብሔር ሊያደርግ ቃል የገባውን ልክ እንዳደረገው ያህል ይናገራል፣ ምክንያቱ እርሱ በእርግጥ ስለሚያደርገው ነው፡፡ "እኔ በእርግጥ ሰጥቼሃለሁ" ወይም "እኔ እሰጣለሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ትንቢታዊ ኃላፊ ጊዜ የሚለውን ይመልከቱ)

የእርሷ ንጉሥ

"እርሷ" የሚለው ቃል የጋይን ከተማ ያመለክታል፡፡ ከተማዎች ብዙውን ጊዜ ሴት እንደሆኑ ተደርጎ ይነገሩ/ይገለጹ ነበር፡፡ "ንጉሥዋ" ወይም "የእነርሱ ንጉሥ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሰውኛ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 8:3

የጦርነት ሰዎች

"የእስራኤል ሰራዊት"

ሰላሳ ሺህ ወንዶች

"30,000 ወንዶች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 8:5

አጠቃላይ መረጃ

ኢያሱ ለወታደሮቹ የጦር ሜዳውን እቅድ መግለጹን ቀጠለ

በእጃችሁ ይሰጣችኋል

እዚህ ስፍራ "እጅ" ምሳሌነቱ እስራኤላውያን በጠላቶቻቸው ላይ ያላቸውን የበላይነት እና ሃይል የሚገልጽ ነው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 8:8

አጠቃላይ መረጃ

ኢያሱ ለወታደሮቹ የጦር ሜዳውን እቅድ መግለጹን አጠናቀቀ፡፡

ኢያሱ ላካቸው

ይህ ሃረግ የሚያመለክተው ኢያሱ በጋይ እንዲያደፍጡ የተመረጡ ሰላሳ ሺህ ወንዶችን መላኩን ነው

የደፈጣው ስፍራ

"ጥቃት የማድረሻው ጊዜ እስኪደርስ ድረስ እነርሱ የሚደበቁበት ስፍራ ነው"

Joshua 8:10

አምስት ሺህ ወንዶች"5,000 ወንዶች"

ይህ ቡድን ከ"ሰላሳ ሺህ ወንዶች" ውስጥ የተወሰደ ይመስላል (ኢያሱ 8፡9)፡፡ 25,000 የሚያህሉት ወንዶች ከተማዋን ሲያጠቁ ይህ አነስ ያለው ቡድን አድፍጦ ቆየ፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 8:13

አጠቃላይ መረጃ፡

እስራኤላውያን ጋይን ለመውጋት ተዘጋጁ

ዋናው ሰራዊት

ይህ በደፈጣ ላይ ከሆኑት ውጭ ያለውን ትልቁን የተዋጊ ቡድን ያመለክታል

ደጀን ጦር

እነዚህ "በከተማይቱ ምዕራብ አቅጣጫ አድፍጠው የተቀመጡ" ናቸው (ኢያሱ 8፡12 ይመልከቱ)

Joshua 8:15

ከእነርሱ አስቀድሞ ራሳቸው ይሸነፉ

"ከጋይ ሰዎች አስቀድሞ ራሳቸው ይሸነፉ" "ከእነርሱ አስቀድሞ" የሚለው ሃረግ የሚወክለው የጋይ ሶች የሚያዩትን እና የሚያስቡትን ነው፡፡ "የጋይ ሰዎች እስራኤላውያን እንደተሸነፉ ያስቡ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ከእነርሱ አስቀድሞ ራሳቸው ይሸነፉ

"ይሸነፉ" የሚለው ሃረግ በአድርጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የጋይ ሰዎች እስራኤላውያንን ያሸነፉ ይምሰላቸው" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ከእነርሱ አስቀድሞ… ተከትለው ሄዱ… እነርሱ ተባረሩ

እዚህ ስፍራ "ከእነርሱ" እና "እነርሱ" የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት የጋይን ሰራዊት ነው፡፡

እነርሱ ሸሹ … ከእነርሱ በኋላ ተከተሉ

እዚህ ስፍራ "ከእነርሱ" እና "እነርሱ" የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት የእስራኤልን ሰራዊት ነው

በከተማይቱ የነበሩ ሰዎች ሁሉ በአንድነት ተጠሩ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የከተማይቱ መሪዎች የከተማይቱን ህዝብ በአንድነት ጠሩ" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

በከተማይቱ የነበሩ ሰዎች ሁሉ

ስለ ሁሉም ሰዎች አጠቃላይ በሆነ መንገድ ይጽፋል፣ ነገር ግን፣ "ሰዎች ሁሉ" የሚለው የሚያመለክተው መዋጋት የሚችሉትን ሰዎች ብቻ ነው፡፡ "በከተማይቱ የነበሩ የእስራኤልን ሰራዊት ማባረር የሚችሉ ሰዎች ሁሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ኩሸት እና ማጠቃለያ የሚሉትን ይመልከቱ፡፡

ክፍት ትተው

"ከተማይቱን ክፍት ትተው"

Joshua 8:24

እስራኤላውያን ሁሉንም የምድሪቱን ነዋሪዎች አጥፍተው ሲጨርሱ… ሁሉም … በሰይፍ ስለት በወደቁ ጊዜ

እዚህ ስፍራ "ወደቁ" የሚለው ሞቱ/ተገደሉ ለሚለው ኢፊሚዝም/የማያስደስትን ቃለ ሻል ባለ ቃል መጠቀም ነው፡፡ እንደዚሁም "የሰይፍ ስለት" የሚለው የሚወክለው ሰይፎችን በሙሉ ሲሆን ሰይፎች የሚለው የሚወክለው አንድም ጦርነትን ወይም የእስራኤልን ሰራዊት ነው፡፡ "በጦርነቱ ውስጥ ሞቱ" ወይም "የእስራኤል ወታደሮች በወጓቸው ጊዜ ሞቱ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ኢፊሚዝም/የማያስደስትን ቃለ ሻል ባለ ቃል መጠቀም እና ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አስራ ሁለት ሺህ

"12,000" ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ

Joshua 8:27

የተተወ ስፍራ

ይህ በአንድ ወቅት ሰዎች የሚኖሩበት፣ አሁን ግን ማንም የማይኖርበት ስፍራ ነው

Joshua 8:29

እስከ ዛሬ ድረስ

"ዛሬ" ወይም "አሁን ድረስ"

Joshua 8:30

የጌባል ተራራ

በከነዓን የሚገኝ ተራራ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 8:34

ሙሴ ካዘዘው ውስጥ ኢያሱ ያላነበበው አንዲትም ቃል እንኳን አልነበረም

ይህ በአዎንታዊ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ሙሴ ያዘዘውን ቃል ሁሉ አነበበ" ወይም "ኢያሱ የሙሴን ህግጋት ሁሉ አነበበ" (ድርብ አሉታዎች)

እስራኤል

ይህ የእስራኤልን መንግስት ያመለክታል


Chapter 9

1 ከዚያም በዮርዳኖስ ማዶ በተራራማውና በቆላማው በታላቁ ባሕር ዳርቻ በሊባኖስም ፊት ለፊት የነበሩ ነገሥታት ሁሉ፥ ኬጢያዊ አሞራዊም ከነዓናዊም ፌርዛዊም ኤዊያዊም ኢያቡሳዊም 2 ኢያሱንና እስራኤልን ሊወጉ አንድ ሆነው ተሰበሰቡ። 3 የገባዖን ሰዎችም ኢያሱ በኢያሪኮና በጋይ ያደረገውን በሰሙ ጊዜ፥ 4 እነርሱ ደግሞ የማታለል ዕቅድ አደረጉ። ራሳችውን እንደ መልእክተኛ አድርገው ቀረቡ። ያረጀና የተቀደደ ጆኒያ ወስደው በአህዮቻቸውም ላይ ጫኑ። ደግሞም ያረጀ፥የተቀደደና የተሰፋ አሮጌ ወይን ጠጅ አቁማዳ ጫኑ። 5 ያረጀ የተሰፋም ጫማ በእግራቸው አደረጉ፤ አሮጌምና የተቀደድ ልብስም ለበሱ። ለስንቅም የያዙት እንጀራ ሁሉ የደረቀና የሻገተ ነበረ። 6 ኢያሱም ወደ ሰፈረበት ወደ ጌልገላ ሄደው ለእርሱና ለእስራኤል ሕዝብ፦በጣም ሩቅ አገር ከሆነ ተጉዘን የመጠን ነን፥ ከእኛ ጋር ኪዳን አድርጉ አሉ። 7 የእስራኤልም ሰዎች ኤዊያውያንን፦ ምናልባት በመካከላችን የምትቀመጡ ትሆናላችሁ። እንዴትስ ከእናንተ ጋር ቃል ኪዳን እናደርጋለን? አሉአቸው። 8 እነርሱም እንዲህ አሉት፦ እኛ የእናንተ አገልጋዮች ነን። ኢያሱም እንዲህ አላቸው፦ እናንተ እነማን ናችሁ? ከወዴትስ መጣችሁ? 9 እነርሱም ለኢያሱ እንዲህ አሉት፦ እኛ አገልጋዮችህ ከእግዚአብሔር ከአምላክህ ስም የተነሣ እጅግ ከራቀ አገር እዚህ መጥተናል። ዝናውንም በግብፅም ያደረገውን ሁሉ፥ 10 በዮርዳኖስ ማዶም በነበሩት በሁለቱ በአሞራውያን ነገሥታት በሐሴቦን በንጉሥ በሴዎን በአስታሮትም በነበረው በባሳን ንጉሥ በዐግ ያደረገውን ሁሉ ሰምተናል። 11 ሽማግሌዎቻችንና በአገራችን የሚኖሩት ሁሉ፦ ለጉዞአችሁም ስንቅ በእጃችሁ ያዙ። ልትገናኙአቸውም ሂዱና እንዲህ በሉአቸው፦ እኛ አገልጋዮቻችሁ ነን፤ ከእኛም ጋር ቃል ኪዳን አድርጉ። 12 ወደ እናንተ ለመምጣት በተነሣንበት ቀን ይህን እንጀራ ትኩስን ለስንቅ ከቤታችን የወሰደነው ነው። ነገር ግን ተመልከቱ፥ አሁንም ደረቅና የሻግብተ ነው። 13 እነዚህም የጠጅ አቁማዳዎች ስንሞላቸው አዲስ ነበሩ፤ እነሆም፥ ተቀድደዋል። ጉዞአችንም እጅግ ሩቅ ስለ ነበረ ልብሶቻችንና ጫማዎቻችን አርጅተዋል። 14 እስራኤላውያንም ከስንቃቸው ወሰዱ፥ ነገር ግን ከእግዚአብሔርም ምክርን አልጠይቁም ነበር። 15 ኢያሱም ከእነርሱ ጋር ስምምነት አደረገ፥ በሕይወት እንዲተዋቸውም ከእነርሱ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። የማኅበሩም አለቆች ከእነርሱ ጋር ቃል ኪዳን አደረጉ። 16 የእስራኤላውያንም ከገባዖን ሰዎች ጋር ቃል ኪዳኑን ካደረጉ ከሦስት ቀን በኋላ፥ ሰዎቹ እዚያው አጠገባቸው የሚኖሩ ጎረቤቶቻቸው መሆናቸውን ዐወቁ። 17 ከዚያም እስራኤላውያን ተዘጋጅተው በሦስተኛው ቀን ወደ ከተሞቻቸው መጡ። የከተሞቻቸውም ስም ገባዖን፥ ክፈራ፥ ብኤሮትና ቂርያትይዓይሪም ናቸው። 18 የሕዝቡም አለቆች በእስራኤል አምላክ በእግዚአብሔር ስም ቃል ኪዳን አድርገው ስለነበረ እስራኤላውያንም ጥቃት አልደረሱባቸውም። የእስራኤልም ሕዝብ ሁሉ በመሪዎቹ ላይ አጉረመረሙ፥ 19 ነገር ግን መሪዎቹ ሁሉ ለማኅበሩ እንዲህ አሉ፦ በእስራኤል አምላክ በእግዚአብሔር ስም ቃል ኪዳን ስለገባንላቸው አሁን ጉዳት ልናደርስባቸው አንችልም፥ 20 የምናደርግላቸው ነገር ቢኖር ይህ ነው፦ የገባንላቸውን የቃል ኪዳን ማሐላ ብናፈርስ ቁጣ እንዳይደርስብን በሕይወት እንዲኖሩ ማድረግ ነው። የሕዝቡም አለቆች ለሕዝባቸው እንዲህ አሉ፦ በሕይወት ይኑሩ። 21 ስለዚህም የእስራኤል አለቆች ስለእነርሱ እንደ ተናገሩት ገባዖናውያን ለእስራኤላውያን ሁሉ እንጨት ሰባሪና ውኃ ቀጂ ሆኑ። 22 ከዚያም ኢያሱ የገባዖንን ሰዎች ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ እናንተ እዚሁ በመካከላችን እየኖራችሁ፥ ከእናንተ ሩቅ ስፍራ ነው የመጠነው፥ ብላችሁ ያታለላችሁን ለምንድን ነው? 23 ስለዚህ በዚህ ምክንያት እናንተ የተረገማችሁ ናችሁ፥ አንዳንዶቻችሁም ለአምላኬ ቤት ሁል ጊዜ እንጨት ሰባሪና ውኋ ቀጂ አገልጋዮች ትሆናላችሁ። 24 እነርሱም ለኢያሱ እንዲህ ብለው መለሱለት፥ እግዚአብሔር አምላክህ አገልጋዩን ሙሴን እንዳዘዘው፥ ምድሪቱን በሙሉ ለእናንተ እንደሚሰጣችሁና ነዋሪዎቿንም ከፊታችሁ እንደሚያጠፋቸው በእርግጥ ለእኛ አገልጋዮችህ ተነግሮናል፥ ስለዚህ ከእናንተ የተነሣ ለሕይውታችን በመሥጋት ይህን አድርገናል። 25 እነሆ አሁን በእጅህ ነን፥ መልካምና ትክክል መስሎ የታየህን ነገር ሁሉ አድርግብን። 26 ስለዚህ ኢያሱ የገባዖንን ሰዎች ከእስራኤል ሰዎች እጅ አዳናቸ እስራኤላውያንም አልገደሏቸውም። 27 በዚያም ዕለት ኢያሱ የገባዖንን ሰዎች ለማኅበረ ሰቡና እግዚአብሔር በመረጠው ስፍራ ለሚቆመው የእግዚአብሔር መሠዊያ እስከ ዛሬ ድረስ እንጨት ሰባሪችና ውኃ ቀጂዎች አደረጋቸው።



Joshua 9:1

የዮርዳኖስ

ለዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)በአንድ እዝ ስር እዚህ ስፍራ "እዝ/አዛዥ" የሚለው የሚወክለው የሚያዛቸውን አዛዥ ነው፡፡ በእርሱ ስር መሆን የሚወክለው የእርሱን ትዕዛዞች መቀበልን ነው፡፡ "የአንድን መሪ ትዕዛዞች መቀበል" በሚለው ውሰጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 9:3

የማታለል እቅድ

ኢያሱን እና እስራኤላውያንን ለማታለል የተደረገ ማጭበርበር

ደረቅ እና የሻገተ

"ደረቅ እና በሻጋታ የተሞላ" ወይም "የሻገተ እና ያረጀ

Joshua 9:6

የእስራኤል ወንዶች

ይህ መላውን የእስራኤል መንግስት ያመለክታል፡፡ (ስኔክቲክ/የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መወከል)

ሖራውያን

ይህ የገባዖናውያን ሌላ ስማቸው ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ምናልባት እናንተ በእኛ አቅራቢያ የምትኖሩ ልትሆኑ ትችላላችሁ፡፡ እንዴት ከእናንተ ጋር ቃል ኪዳን መግባት እንችላለን?

ኢያሱ የእስራኤል ህዝብ ከማናቸውም ነገር በላይ ለያህዌ ትእዛዝ ትኩረት ሰጥተው መከተል እንዳለባቸው ትኩረት ይሰጣል፡፡ "በእኛ አቅራቢያ የምትኖሩ ከሆናችሁ፣ ከእናንተ ጋር ቃል ኪዳን መግባት አንችልም" (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 9:9

የዮርዳኖስ

ለዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሴዎን

ይህ የተሸነፈው የአሞራውያን ንጉሥ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሔሴቦን

x

Joshua 9:11

በእጃችሁ

የዚህ ሃረግ ትረጉም "ይዛችሁ ሂዱ" የሚል ነው፡፡ እዚህ ስፍራ "እጅ" የሚለው ቃል የሚወክለው ከአቅርቦት ውስጥ ገባዖናውያን ያላቸውን ነው፡፡ (ስኔክቲክ/የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር ወከል)አግኟቸውና እንዲህ በሏቸው "እነሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእስራኤልን ሰዎች ነው

Joshua 9:14

ኢያሱ አብረዋቸው ይኖሩ ዘንድ ከእነርሱ ጋር ሰላምን እና ቃልኪዳንን አደረገ፡፡ እንደዚሁም የህዝቡ መሪዎችም ለእነርሱ ቃለመሃላ አደረጉ፡፡

እነዚህ ሁለት ዐረፍተ ነገሮች ተመሳሳይ ነገር መደረጉን ይናገራሉ፡፡ የእስራኤል ህዝብ መሪ ኢያሱ፣ ገባዖናውያንን እንደማይገድል ቃል ገባ፡፡ የእስራኤል ህዝብ መሪዎችም በተመሳሳዩ ይህንኑ ቃል ኪዳን ገቡ፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

ህዝቡ

እዚህ ስፍራ ይህ ቃል የሚያመለክተው የእስራኤልን ህዝብ ነው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 9:16

ሶስተኛ ቀን

ይህ በቅደም ተከተል ቁጥር ሶስትን ያመለክታል (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ከፊራ

ይህ ከገባዖን ከተሞች አንዱ ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ብኤሮት

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ቂርያትይዓይሪም

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 9:18

ህዝቡ

እዚህ ስፍራ ይህ ቃል የሚያመለክተው የእስራኤልን ህዝብ ነው፡፡

Joshua 9:20

"ገባዖናውያን እንጨት ቆራጮች እና ውሃ ቀጂዎች ሆኑ"

"ገባዖናውያን እንጨት ቆራጮች እና ውሃ ቀጂዎች ሆኑ"

Joshua 9:22

የአምላኬ ቤት

እዚህ ይህ ሃረግ የሚያመለክተው የማደሪያውን ድነኳን፣ የያህዌን ማደሪያ ስፍራ ነው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 9:24

መልካም እና ትክክል የሚመስለውን ሁሉ

"መልካም" እና "ትክክል" የሚሉት ቃላት በመሰረቱ አንድ አይነት ነገር ማለት ናቸው፡፡ "ተገቢ እና ትክክል የሚመስልህን ሁሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ጥንድ ትርጉም የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 9:26

ለእነርሱ

እዚህ ስፍራ "እነርሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ገባዖናውያንን ነው፡፡እስከዚህ ቀን ድረስ "እስከ አሁን ድረስ እንኳን፡፡" ይህ ማለት ህዝቡ እነዚህን ነገሮች ጸሐፊው ይኖር እስከ ነበረበት ጊዜ ድረስ ጭምር ማድረጋቸውን ቀጥለው ነበር ማለት ነው


Chapter 10

1 የኢየሩሳሌም ንጉሥ አዶነጼዴቅ ኢያሱ ጋይን ይዞ ፈጽሞ እንደ ደመሰሳት፤ እንደዚሁም በኢያሪኮና በንጉሥዋ ላይ ያደረገውን ሁሉ ሰማ። እንዲሁም የገባዖን ሰዎች ከእስራኤል ጋር እንዴት የሰላም ውል አድርገው በመካከላቸው መኖራቸውን ሰማ። 2 የኢየሩሳሌም ሕዝብ ፈሩ፥ ምክንያቱም ገባዖን እንደ ነገሥታቱ ከተማ ሁሉ ታላቅ ከተማ ነች። ገባዖንም ከጋይ ይልቅ ትልቅና ሰዎቿም ብርቱ ተዋጊዎች ነበሩ። 3 ስለዚህ የኢየሩሳሌም ንጉሥ አዶኒጼዴቅ፥ ወደ የኬብሮን ንገሥ ሆነም፥ ወደ የያርሙት ንጉሥ ጲርአም ፥ ወደ የለኪሶ ንጉሥ ያፈዓና ወደ የዔግሎን ንጉሥ ዳቤር ላከ። 4 ወደዚህ መጥታችሁ አግዙኝ። ገባዖን ከኢያሱና ከእስራኤላውያን ጋር የሰላም ስምምነት ስላደረጉ ገባዖንን እንምታ። 5 ከዚያም አምስቱ የአሞራውያን ነገሥታት ማለት የኢየሩሳሌም ንጉሥ፥ የኬብሮን ንጉሥ፥ የያርሙት ንጉሥ፥ የለኪሶ ንጉሥና የዔግሎን ንጉሥ ያላቸውን ሠራዊታቸውን ሁሉ አስተባብረው፥ ገባዖንን ወጓት። 6 የገባዖንም ሰዎች ወደ ኢያሱና ወደ ጌልገላ ሠራዊት መልእክት ላኩ። እንዲህም አሉ፦ ከአገልጋዮቻችሁ እጃችሁን አታውጡ ፍጠኑ። በፍጥነት መጥታችሁ አድኑን። በተራራማው አገር የሚኖሩ የአሞራውያን ነገሥታት ሁሉ ኃይላቸውን አስተባብረው እኛን ለማጥቃት ተሰልፈውብናልና እርዱን። እኛን ባሮችህን አትተወን ርዳን ፈጥነህ በመድረስም አድነን ብለው ላኩበት። 7 ስለዚህ ኢያሱ እርሱና ተዋጊዎች ሰዎች ሁሉ ከእርሱ ጋር ጨምሮ ከጌልገላ ወጣ። 8 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ አለ፦ አትፍራቸው። በእጅህ አሳልፌ ሰጥቻለሁ፤ ማንም ሊቋቋሙህ አይችልም። 9 ኢያሱም ከጌልገላ ሌሊቱን ሁሉ ሲገሠግሥ አድሮ ድንገት ደረሰባቸው። 10 እግዚአብሔም የጠላትን ሠራዊት በእስራኤል ፊት ግራ አጋባቸው። እጅግ መታቸው። በገባዖንም ወደ ቤት ሖሮን በሚያስወጣው መንገድ እስከ ዓዜቅ መንገድ እስከ መቄዳም ድረስ ተከትሎአቸው አሳድዶ መታቸው። 11 ከቤት ሖሮን ወደ ዓዜቃ ቁልቁል በሚወስደው መንገድ ላይ ከእስራኤላውያን ፊት በሚሽሹበት ጊዜ እግዚአብሔር ከሰማይ ትልልቅ ድንጋዮች ወረወረባቸው ሞቱም። በእስራኤል ሰዎች ሰይፍ ከሞቱት ይልቅ በወረደው የበረዶ ድንጋዮች የሞቱት የበለጡ ነበሩ። 12 ከዚያም እግዚአብሔር ለእስራኤል በአሞራውያን ላይ ድል በሰጠበት ዕለት ኢያሱ እግዚአብሔርን ተናገረ። ኢያሱም በእስራኤል ፊት እግዚአብሔርን እንዲህ አለው፦ "ፀሐይ፥ በኤሎን ሸለቆ በገባዖን ላይ ይቁም።" 13 ሕዝቡ ጠላቶቹን እስኪ በቀል ድረስ፤ ፀሐይ ባለችበት ቆመች፥ ጨረቃም አልተንቀሳቀሰችም። ይህም በያሻር መጽሐፍ ላይ የተጻፈ አይደለምን? ፀሐይ በሰማዩ መካከል ቆመች፥ ለሙሉ ቀን ያህል አልተንቀሳቀሰችም ነበር። 14 እግዚአብሔር የሰውን ቃል እንደዚያ የሰማበት ዕለት ከዚያ በፊት ወይም ከዚያ በኋላ አልነበረም። እግዚእአብሔር ለእስራኤል ይዋጋ ነበር። 15 ኢያሱና መላው እስራኤል ወደ ጌልገላ ሰፈር ተመለሱ። 16 በዚህ ጊዜ አምስቱ የአሞራውያን ገሥታት ሸሽተው በመቄዳ ዋሻ ራሳቸውን ደብቀው ነበር። 17 ኢያሱም አምስቱ ነገሥታት በመቄዳ ዋሻ ውስጥ ተደብቀው መገኘታቸውን ሰማ፤ 18 ኢያሱም እንዲህ አለ፦ ትልልቅ ድንጋዮች ወደ ዋሻው አፍ አንከባልሉ፤ወታደሮችንም እንዲጠብቁአቸው በዚያ አቁሙ። ቸልም አትበሉ። 19 ጠላቶቻችሁን አሳዱአቸው፤ ከበስተ ኋላ ሆናችሁም ጥቃት አድርሱባቸው። እግዚአብሔር አምላካችሁ በእጃችሁ አሳልፎ ስለሰጣችሁ ወደ ከተሞቻቸው እንዳይገቡ አድርጉአቸው። 20 ኢያሱና እስራኤል ልጆች ፈጽሞ እስኪያጠፉ ድረስ ከታላቅ ጭፍጨፋ ጋር ጨረሱ። የተረፉት ጥቂቶቹ ብቻ ወደ ተመሸጉት ከተሞቻቸው ደረሱ። 21 ከዚያም ሠራዊቱ በሙሉ በደኅና ተመልሶ ኢያሱ ወደ ሰፈረበት ወደ መቄዳ ተመለሰ። በእስራኤላውያንም ላይ አንድት ቃል ለመናገር ማንም ሰው የደፈረ አልነበረም። 22 ኢያሱም እንዲህ አላቸው፦ የዋሻውንም አፍ ክፈቱና ከዋሻው እነዚህን አምስቱን ነገሥታት አምጡልኝ። 23 እነርሱም እንዳለው አደረጉ። እነዚህንም አምስቱን ነገሥታት፦ የኢየሩሳሌምን ንጉሥ፥ የኬብሮንን ንጉሥ፥ የያርሙትን ንጉሥ የለኪሶን ንጉሥና የዔግሎንን ንጉሥ አውጥተው አመጡለት። 24 እነዚህን ነገሥታት ወደ ኢያሱ ባማጡበት ጊዜ፥ እርሱም እያንዳንዱን የእስራኤል ሰዎች ጠራቸው፤ እንዲሁም ከእርሱ ጋር ወደ ጦርነት ሄደው የነበሩትን የጦር አዛዦችን እንዲህ አላቸው፦ እግሮቻችሁን በእነዚህ ነገሥታት አንገት ላይ አድርጉ። እነርሱም ወደ ፊት ቀርበው እግሮቻቸውን በነገሥታቱ አንገት ላይ አሳረፉ። 25 ኢያሱም እንዲህ አላቸው፦ አትፍሩ፥ አትደንግጡም። በርቱ፥ ጽኑም። እግዚአብሔር አምላካችሁ በምትዋጉበት ጊዜ በጠላቶቻችሁ ሁሉ ላይ እንዲህ ያደርጋል። 26 ከዚያም ኢያሱ ነገሥታቱን መትቶ ገደላቸው። በአምስትም ዛፎች ላይ ሰቀላቸው። አስክሬናቸውም እስኪመሽ ድረስ ተሰቅለው ነበር። 27 የፀሐይ መጥለቂያ በሆነ ጊዜ ኢያሱ ትእዛዝ ሰጠ፦ ከዚያም የነገሥታቱን አስክሬኖች ከዛፎቹ ላይ እንዲያወርዱ ቀድሞ ራሳቸውን ደብቀው ወደነበሩበት ዋሻ ውስጥ እንዲጥሉአቸው አዘዛቸው። በዋሻውም አፍ ላይ ትልልቅ ድንጋዮች አኖሩ። እነዚያ ድንጋዮች እስከ ዛሬ ድረስ በዚያ ይገኛሉ። 28 በዚህ መንገድ በዚያች ዕለት ኢያሱ መቄዳን ያዘ፤ ከንጉሥዋም ጭምር ሁሉንም በሰይፍ ገደለ። በሕይወት ያሉትንም ፍጥረት ሁሉ ምንም ሳያስቀር ፈጽሞ አጠፋቸው። በኢያሪኮ ንጉሥ ላይ ያደረገውንም ሁሉ፥ በመቄዳ ንጉሥ ላይ አደረገ። 29 ኢያሱና እስራኤላውያን ከመቄዳ ወደ ልብና አለፉ። ወጓትም። 30 እንደገናም ከልብና ጋር ጦርነት ገጠሙ። እግዚአብሔርም ከተማይቱንና ንጉሥዋን በእስራኤል እጅ አሳልፎ ሰጣቸው። ኢያሱም በተከማዪቱንና በውስጧ ያለውን ሕይወት ያለውን ፍጥረት ሁሉ በሰይፍ ስለት አጠፋ። ሕይወት ያለውን ምንም አላስቀረም። በኢያሪኮ ንጉሥ ላይ ያደረገውንም በልብና ንጉሥ ላይ አደረገ። 31 ከዚያም ኢያሱና እስራኤላውያን ከእርሱ ጋር ከልብና ወደ ለኪሶ አለፉ። በእርስዋም ሰፈሩ፤ ጦርነትም አደረጉ። 32 እግዚአብሔርም ለኪሶን በእስራኤል እጅ አሳልፎ ሰጠው። ኢያሱም በሁለተኛው ቀን ያዛት። በልብና እንዳደርገው በሕይወት ያለውን ፍጥረት ሁሉ በሰይፍ ስለት አጠፋ። 33 ከዚያ የጌዝር ንጉሥ ሆራም ለኪሶን ለመርዳት መጣ። ኢያሱ ግን አንድ እንኳ ሳያስተርፍ እርሱንና ሕዝቡን መታቸው። 34 ከዚያም ኢያሱና እስራኤላውያን በሙሉ ከለኪሶን ወደ ዔግሎን አለፉ። እዚያም ሰፈሩ፤ ወጓትም፤ 35 በዚያኑ ዕለት ከተማዋንም ያዟት። ኢያሱም በለኪሶ እንዳደረገ ከተማይቱንና በውስጧ የሚገኙትን ፈጽመው በሰይፍ ስለት አጠፏት። 36 ከዚያም ኢያሱና እስራኤላውያን ከዔግሎን ወደ ኬብሮን አለፉ። በከተማይቱም ጦርነት አደረጉ። 37 ከተማዪቱንም ከንጉሥዋ ከመንደሮቿና በውስጧ ካሉት ጭምር ሁሉ አንድም ሰው ሳያስቀሩ በሰይፍ ስለት አጠፉአቸው። በዔግሎን እንዳደርጉት ሁሉ ከተማዪቱንና በውስጧ ያለውን ሁሉ ፈጽመው ደመሰሱ። ማንኛውንም ሕይወት ያለውን ፍጥረት ሁሉ አጠፋ። 38 ከዚያ ኢያሱና እስራኤል ሠራዊት ከእርሱ ጋር ወደ ኋላ ተመልሰው በደቤርን አለፉ፤ ጦርነቱንም አደረጉ። 39 ከተማዪቱን ንጉሥዋንና በአካባቢ ያሉ መንደሮቿን ሁሉ ያዙ። ከተማይቱንና በውስጧ ያለውንም ሁሉ አንድም ሰው ሳያስቀሩ፥ በሰይፍ ስለት አጠፉአቸው። ኢያሱ በኬብሮን ያደረጉትን ሁሉ በዳቤርና በንጉሥዋ ላይ አደረጉት። 40 ኢያሱ ተራራማውን አገር ኔጌቭን ቆላና የተራራውን ሸንተረሮች ጨምሮ ምድሪቱን በሙሉ ከነገሥታቷ ጋር አሸነፈ። ከነገሥታቱንም ያስቀረው ማንም የለም። የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረትሕይወት ያላቸውን ሁሉ ፈጽሞ አጠፋቸው። 41 ኢያሱም ከቃዴስ በርኔ እስከ ጋዛ፥ የጎሶምን ምድር ሁሉ እስከ ገባዖን ድረስ በሙሉ አጠፋ። 42 ኢያሱ እነዚህን ሁሉ ነገሥታትና ምድራቸውን የያዘው በአንድ ጊዜ፥ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ስለተዋጋ ነው። 43 ኢያሱ ከመላው እስራኤላውያን ጋር ጌልገላ ወዳለው ሰፈር ተመለሰ።



Joshua 10:3

የርሙት… ለኪሶ.. ዔግሎ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሆሃም... ጲርአም… ያፊዓ..ዳቤር

እነዚህ የንጉሦች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ እኔ ና

"እኔ ወዳለሁበት ተጓዝ፡፡" ኢየሩሳሌም በከነአን ለሚገኙ ከተሞች ሁሉ ከፍ ባለ ስፍራ ላይ የምትገኝ ከተማ ነበረች፡፡

Joshua 10:5

አምስት ንጉሦች

"5 ንጉሦች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የርሙት… ለኪሶ.. ዔግሎ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

አሰፋፈራቸውን ከገባዖን በተቃራኒ አደረጉ

ይህ ማለት ሰፈራቸውን በከተማቸው ዙሪያ አደረጉ፡፡ ይህ በከተማይቱ የሚኖሩትን ማዳከሚያ መንገድ ነበር፡፡ ድርጊቱ ሰዎች ከከተማይቱ እንዳያመልጡ ያግዳል፣ እንደዚሁም ሌሎች ምግብ እና ውሃ ወደ ከተማይቱ እንዳያመጡላቸው ያግዳል፡፡

Joshua 10:6

እነርሱ እንዲህ አሉ

"እነርሱ" የሚለው ቃል እዚህ ስፍራ የሚያመለክተው ገባዖናውያንን ነው፡፡

እጆችህን ከባሪያዎችህ አታርቅ/አታንሳ

ይህ ትሁት ልመና በሁለት አሉታዎች ተገልጾዋል፣ ይህም አዎንታዊ ድርጊት/እርዳታ ማስፈለጉን በአጽንኦት ለመግለጽ ነው፡፡ "እባክህ መጥተህ በብርቱ እጆችህ ታደገን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ምፀት/ላይዶክስ የሚለውን ይመልከቱ)

እጆችህ

እዚህ ስፍራ "እጆች" የሚለው ቃል የእስራኤልን ህዝብ ጥንካሬ ያመለክታል፡፡ "የአንተ ጥንካሬ" (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:8

እነርሱን በእጆችህ አሳልፌ ሰጥቼሃለሁ

እዚህ ስፍራ "እጅ" የሚለው የሚወክለው የእስራኤልን ህዝብ ጥንካሬ እና ጠላቶቻቸውን የማሸነፍ አቅማቸውን ነው፡፡ "እነርሱ" የሚለው ቃል አጥቂ የሆነውን ሰራዊት ያመለክታል፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

እኔ ለእነርሱ ሰጥቻቸዋለሁ

እዚህ ስፍራ "እነርሱ" የሚለው ቃል ጥቃት የሚጥለውን ሰራዊት ያመለክታል፡፡

Joshua 10:9

ኢያሱ መጣ

እዚህ ስፍራ መላው የእስራኤል ሰራዊት የተጠቀሱት በመሪያቸው በኢያሱ ነው፡፡ (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚለውን ይመልከቱ)ያህዌ በእስራኤል ፊት ጠላቶቻቸውን ግራ አጋባቸው እዚህ ስፍራ "እስራኤል" የሚለው መላውን የእስራኤል ሰራዊት ያመለክታል፡፡ ቤትሖሮን… ዓዜቅ… መቄዳም እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:11

ቤትሖሮን… ዓዜቅ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ከላይ ከሰማይ ትላልቅ ድንጋይ አወረደባቸው

"ከሰማይ የበረዶ ድንጋይ አወረደባቸው"

Joshua 10:12

ፀሐይ በገባዖን ትቁም፣ ጨረቃም በኤሎን ሸለቆ ትቁም

ኢያሱ በዚህ ቀን ጊዜ ያህዌ ጊዜ መንቀሳቀሱን እንዲያቆም ጸለየ፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን መልከቱ) ፀሐይ… ጨረቃ ኢያሱ ፀሐይን እና ጨረቃን እንደ ሰው አዘዛቸው፡፡ (ሰውኛ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ) የኤሎን ሸለቆ ይህ የቦታ ስም ነው (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:13

ሃገሪቱ

ይህ የእስራኤልን ህዝብ ያመለክታል (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ በያሻር መጽሐፍ የተጻፈ አይደለምን?

ጸሐፊው ይህንን ጥያቄ ትዕይንቱ በሚገባ መመዝገቡን ለአንባቢው ለማስታወስ እንደ መረጃ ዳራ ተጠቅሞበታል፡፡ "ይህ በያሻር መጽሐፍ ተጽፏል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ እና የመረጃ ዳራ የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 10:15

መቄዳ

ይህ የከተማ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ለኢያሱ ተነግሮት ነበር

መልዕክተኞች መጥተው ለኢያሱ ነገሩት፡፡ "አንድ ሰው ለኢያሱ ነገረው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ተመልከቱ)

Joshua 10:18

በእናንተ እጅ

"በእጃችሁ" የሚለው ሀረግ ትርጉሙ "ማድረግ የምትችሉት" ማለት ነው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:20

መቄዳ

በኢያሱ 10፡10 ውስጥ በተረጎሙት መሰረት ይተርጉሙ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በመቃወም አንድም ቃል ለመናገር የቻለ የለም

"ማንም አንዳች ነገር በመቃወም መናገር አልደፈረም" ወይም "ማንም ለማማረር ወይም ለመቃወም አልደፈረም"

Joshua 10:22

የዋሻውን አፍ ክፈቱ

እዚህ ስፍራ "አፍ" የሚለው ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ትርጉሙ "መግቢያ" ማለት ነው፡፡ "የዋሻውን መግቢያ ክፈቱ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የርሙት… ለኪሶ.. ዔግሎ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው (ስሞች እንዴት ይተጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:24

እያንዳንዱ የእስራኤል ሰው

በዚህ ስፍራ የእስራኤል ሰዎች የሚለው የሚወክለው ወታደር የሆኑትን ብቻ ነው፡፡ (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ ማለውን ነገር መወከል የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:26

እስከ ዛሬ ድረስ

"ጸሐፊው ይህንን ታሪክ እስከጻፈ ድረስ"

Joshua 10:28

መቄዳ

ይህ የከተማ ስወም ነው፡፡ ይህንን በኢያሱ 10፡10 ውስጥ እንዴት እንደ ተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)በውስጧ የሚገኙትን ሙሉ በሙሉ ደመሰሰ፡፡ አንድም ነገር በህይወት አላስቀረም፡፡ ኢያሱ አንድም ሰው ወይም እንስሳ በህይወት አለማስቀረቱን ትኩረት ሰጥቶ ለመግለጽ፣ ሁለተኛው ዐረፍተ ነገር የመጀመሪያውን አረፍተ ነገር አጠቃሎ ያቀርባል፡፡

Joshua 10:29

ልብና

ይህ የከተማ ስወም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በእስራኤል እጀ አሳልፎ ሰጣት

እዚህ ስፍራ "እጅ" የሚለው "መቆጣጠር" ማለት ነው፡፡ "ለእስራኤል አሳልፎ ሰጣት" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:31

ልብና…ለኪሶ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በእስራኤል እጀ

እዚህ ስፍራ የእነርሱ "እጅ" የሚለው የሚወክለው የእነርሱን የበላይነት/መቆጣጠር ነው፡፡ "ያህዌ ለኪሶን ለእስራኤል መንግሥት አሳልፎ ሰጠ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:33

ሆራም

ይህ ታላቅ የሆነ ንጉሥ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ጌዝር… ለኪሶ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:34

ለኪሶ…ዔግሎን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በሰይፍ ስለት ምቷት… በውስጧ የሚኖሩትንም ሁሉ ሙሉ ለሙሉ አጥፉ

እነዚህ ሁለት ሀረጋት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፡፡ በአንድነት የዔግሎን ከተማ ሙሉ ለሙሉ መጥፋትን ይገልጻሉ፡፡ (ጥንድ ትርጉም የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:36

ዔግሎን

ይህ የከተማ ስወም ነው፡፡ ይህንን በኢያሱ 10፡3 ውስጥ እንዴት እንደ ተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ከተማቱን ይዘው በሰይፍ ስለት ምቷት

ሰይፉ የሚወክለው የእስራኤልን ሰራዊት ነው፣ መምታት የሚለው የሚገልጸው የማረድ እና የመደምሰስ ሃሳብን ነው፡፡ "ያዙ፣ገደሉ፣ ደመሰሱ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:38

ዳቤር… ልብና

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

እነርሱን በሰይፍ ስለት መቷቸው

ሰይፉ የሚወክለው የእስራኤልን ሰራዊት ነው፣ መምታት የሚለው የሚገልጸው የማረድ እና የመደምሰስ ሃሳብን ነው፡፡ "ገደሉ ደግሞም ደመሰሷቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:40

ከንጉሦቻቸው ውስጥ አንድ እንኳን በህይወት አላስቀረም፡፡ በህይወት ያለውን ነገር ሁሉ ሙሉ ለሙሉ ደመሰሰ

እነዚህ ሁለት ሃረጋት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፤ሃረጎቹ የእስራኤል ህዝብ በያህዌ ትዕዛዝ የፈጸመውን ሙሉ ለሙሉ የመደምሰስ ተግባር ያጎላሉ፡፡ (ትይዩ ንጽጽር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 10:42

ኢያሱ እነዚህን ነገሥታት ሁሉ ማረከ እና አገራቸውንም ያዘ፡፡

ይህ በኢያሱ 10፡28 ጀምሮ የተዘረዘሩትን ነገሥታት እና ምድራቸውን ያመለክታል

ኢያሱ ማረከ

እዚህ ስፍራ ኢያሱ የሚወክለው ጠቅላላውን ሰራዊቱን ነው፡፡ "ኢያሱ እና ወታደሮቹ ማረኩ/ያዙ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ስኔክቲክ/የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ)

በአንድ ጊዜ

ይህ በአንድ ቀን ማለት አይደለም፡፡ በርካታ ቀናት ወይም ሳምንታት ሊወስድ በሚችል በአንድ ወታደራዊ ዘመቻ ወቅት ማለት ነው፡፡


Chapter 11

1 የአሦርም ንጉሥ ኢያቢስ ይህን በሰማ ጊዜ፥ ወደ ዮባብ ንጉሥ፥ ወደ ማዶን ንጉሥ፥ ወደ ሺምሮን ንጉሥና ወደ አዚፍ ንጉሥ መልእክት ላከ። 2 ደግሞም በሰሜናዊ በተራራማው አገር፥ በየርዳኖስ ወንዝ ሸለቆ ከኪኔሬት በስተ ደቡብ ፥ በምዕራቡ ቆላማ አገሮችና ከኮር ኮረብታማ በስተ ምዕራብ ወዳሉት ነገሥታት ላከ። 3 በምሥራቅና በምዕራብ ወደሚገኙት ወደ ከነዓናውያንም፥ ወደ አሞራውያን፥ ወደ ኬጢያውያን፥ ወደ ፌርዛውያንና በኮረብታማው አገር ወደሚኖሩት ወደ ኢያቡሳውያን እንዲሁም በምጽጳ ምድር በአርሞንዔም ተራራ ወዳሉት ወደ ኤዊያውያን ነገሥታት መልእክት ላከ። 4 እንዚህም ሠራዊቶቻቸው ሁሉ በቁጥርም በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ እጅግ ከብዙ ወታደሮች ጋር መጡ። ታላቅም ቁጥር ፈረሶችና ሠረገሎች ነበሩአቸው። 5 እነዚህ ሁሉ ነገሥታት እስራኤልን ለመውጋት ኃይላቸውን አስተባብረው በማሮን ውሃ አጠገብ በተቀጠረው ጊዜ ሰፈሩ። 6 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዲህ አለው፦ እነዚህን ሁሉ ነገ በዚች ሰዓት እንደ ሙት አድርጌ በእስራኤል እጅ አሳልፌ ስለምሰጣቸው አትፍራቸው። የፈረሶቻቸውንም ቋንጃ ትቆርጣለህ፥ ሠረገሎቻቸውንም ታቃጥላለህ። 7 ኢያሱና ሠራዊቱ ሁሉ መጡ። በድንገትም ወደ ማሮን ውሃ መጥተው ጠላቶቻቸውን አጠቁኣቸው። 8 እግዚአብሔርም ጠላትን በእስራኤል እጅ አሳልፎ ሰጣቸው። በሰይፍም ስለት አጠቁአቸው፥ ወደ ሲዶና፥ወደ ማስሮን፥ ምጽጳ ሸለቆ ድረስ በስተምሥራቅ አሳደዷቸው። ከእነርሱም በሕይወት አንድንም ሰው ሳያስቀሩ በሰይፍ ስለት አጠፉአቸው። 9 ኢያሱም እግዚአብሔር እንዳዘዘው በእነርሱ ላይ አደረጉ። የፈረሶቻቸውንም ቋንጃ ቆረጠ፥ ሠረገሎቻቸውንም አቃጠለ። 10 በዚያን ጊዜም ኢያሱ ወደ ኋላ ተመልሶ አጾርን ያዘ። ንጉሥዋንም በሰይፍ ገደለው። (አጾርም የእነዚህ መንግሥታት ሁሉ የበላይነት ነበራች።) 11 በውስጧ ያሉትን ሁሉ በሰይፍ ስለት ገደሉ፥ በሕይወት ካለው ፍጡር አንድ እንኳ ሳያስቀሩ ሁሉንም ደመሰሱ። አሦርንም በእሳት አቃጠሏት። 12 ኢያሱም የእነዚህን ነገሥታት ከተሞች በሙሉ ያዘ። ነገሥታታቸውን ሁሉ ማረካቸው፥ በሰይፍም ስለት አጠፋቸው። የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ እንዳዘዘው በሰይፍ ስለት አጠፋቸው። 13 እስራኤልም በተራራው ላይ ከተሠሩ ከተሞች ከአጾር በስተቀር ሌሎችን አላቃጠሉም። ኢያሱ ይህችን ለብቻዋ አቃጠላት። 14 እስራኤላውያንም ምርኮውን በሙሉ ከእነዚህም ከተሞች የተገኙትን እንስሳት ለራሳቸው ወሰዱ። ሕዝቡን በሙሉ ሁሉም ሙት እስኪሆኑ ድረስ በሰይፍ ስለት ገደሉአቸው። በሕይወት ካለው ፍጡር አንድም አልቀሩም። 15 እግዚአብሔር አገልጋዩን ሙሴን እንዳዘዘው ሁሉ ሙሴም ኢያሱን አዘዘው። ኢያሱም እግዚአብሔር ሙሴን ካዘዘው ሁሉ እርሱ ያልፈጸመው አንዳች ነገር አልነበረም። 16 ኢያሱም ማለት ተራራማውን አገር፥ ኔጌቭን ሁሉ፥ የጎሶምን ምድር በሙሉ፥ የኮረብታ ግርጌ። የዮርዳኖስ ወንዝ ሸለቆ፥ የእስራኤልም ኮረብታማ አገርና ቆላማውን የምዕራቡን ቆላዎችን ሁሉ፥ያንን ምድር በሙሉ ወሰደ። 17 እንዲሁም እስከ ሴይር በሚደርሰው ከሐላቅ ተራራ አንሥቶ ከአርሞንዔም ተራራ በታች በሊባኖስ ሸለቆ ውስጥ እስካለው እስከ በዓል ጋድ ድረስ ያለውን ምድር በሙሉ ያዘ። ነገሥታታቸውንም ሁሉ ያዘ፥ መትቶም ገደላቸው። 18 ኢያሱ ከእነዚህ ነገሥታት ጋር ረጅም ጊዜ ጦርነት አደረገ። 19 በገባዖን ከሚኖሩ ከኤዊያውያን በስተቀር ከእስራኤላውያን ጋር የሰላም ስምምነት ያደረገ አንድም ከተማ አልነበረም። እስራኤል ሁሉንም ከተሞች የያዙት በጦርነት ነበር። 20 እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘው ያለ አንዳች ርኅራኄ ፈጽሞ ይደመስሳቸው ዘንድ እስራኤልን እንዲወጉ ልባቸውን ያደነደናቸው ራሱ እግዚአብሔር ነበር። 21 በዚያንም ጊዜ ኢያሱ መጥቶ ዔናቅን አጠፋ። ይህንንም በተራራማው አገር በኬብሮን፥ በዳቤርና በአናብ እንዲሁም በመላው ይሁዳና የእስራኤል ተራራማ አገሮች ያሉትን ላይ አደረገ። እርሱም እነርሱንና ከተሞቻቸውን በሙሉ አጠፋቸው። 22 ከእነዚህም ጥቂቶቹ ብቻ በጋዛ፥ በጌትና በአሽዶድ ከቀሩት በስተቀር በእስራኤል አገር ከዓናቅ የቀሩት አልነበሩም። 23 ስለዚህ ኢያሱ እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘው ምድሪቱን በሙሉ ያዘ። ኢያሱም እንደ ነገዳቸው አከፋፈል በመመደብም ርስት አድርጎ ለእስራእላውያን ሰጣቸው። ከዚያም ምድሪቱ ከጦርነት ዐረፈች።



Joshua 11:1

ያቢን…ዮባብ

እነዚህ የንጉሦች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሃዞር.. ማዶን… ሺምሮን… አዚፍ… ኪኔሬት.. ናፎት ዶር … ሄርሞን ተራራ

እነዚህ የስፍራ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 11:4

አጠቃላይ መረጃ፡

ሁሉም የከነዓን ንጉሦች በኢያሱና በእስራኤል ላይ ዘመቱ

ብዙ ቁጥር ያለው ሰራዊት ፣ በቁጥር እንደ ባህር ዳርቻ አሸዋ የበዛ

ማንም የባህር ዳርቻ አሸዋን መቁጠር አይችልም፡፡ ይህ ግነት የሚያገላው እነዚህ ነገሥታት የሰበሰቧቸውን ወታዶች ብዛት ነው፡፡ "በወንዝ ዳርቻ እንደሚገኝ አሸዋ እንዲህ ያለ ታላቅ ቁጥር ያለው ወታደር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ኩሸት እና ማጠቃለያ የሚሉትን ይመልከቱ)

ማሮም

ይህ የስፍራ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 11:6

እኔ ለእስራኤል ሁሉንም እንደ ሞተ ሰው አሳልፌ ሰጥቻቸዋለሁ

እስራኤ ጠላቶቹን ለመማረክ እና ሁሉንም ለመደምሰስ ያስቻለው ያህዌ የእስራኤል ጠላት የሆኑትን ወታደሮች በሙሉ ከገደለ በኋላ አሳልፎ እንደሰጣቸው ተደርጎ ተገልጽዋል፡፡ " እስራኤል ጠላቶቹን ሁሉ እንዲያጠፋ አሳልፌ እሰጠዋለሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የፈረሶቻቸውን ቋንጃ ይቆርጣሉ

"እግሮቻቸውን በመቁረጥ ፈረሶቻቸውን ስንኩል ማድረግ" ይህ ከፈረሶቹ እግር በስተኋላ ያልን ጅማት በመቁረጥ ፈረሶቹ መራመድ እንዳይችሉ የማድረግ ልምምድ ነው፡፡

ማሮም

ይህ የስፍራ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 11:8

ያህዌ ለእስራኤላዊያን ጠላቶቻቸውን በእጃቸው አሳልፎ ሰጣቸው

እዚህ ስፍራ "እጅ" የሚለው ቃል የሚወክለው ሃይልን ነው፡፡ ያህዌ የእስራኤል ሰራዊት ጠላቶቻቸውን እንዲማርኩ ማድረጉ የተገለጸው ልክ ጠላቶቻቸውን በእጃቸው ላይ እንዳስቀመጠ ተደርጎ ነው፡፡ "ያህዌ እስራኤል ጠላቶቹን እንዲማርክ አሳልፎ ሰጠው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡

ምቷቸው.. ምቷቸው

"አጥቋቸው… አጥቋቸው"

ማስሪፎት/ማስሮን ሜም

ይህ የስፍራ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ቋንጃ መቁረጥ

ይህ ፈረሶቹ መሮጥ እንዳይችሉ ያኋላ እግራቸው ጅማት የተቆረጠበት ልምምድ ነው፡፡ ይህንን ቃል በኢያሱ 11፡6 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡

Joshua 11:10

ንጉሥዋን በሰይፍ መታ

"ኢያሱ የሐጾርን ንጉሥ በሰይፍ ገደለ"

ሐጾር የእነዚህ መንግሥታት ሁሉ ራስ ነበር

የሐጾር ከተማ ታላቅነት የተገለጸው ሐጾር የእነዚህ መንግሥታት ሁሉ ራስ ነበር በሚል ነው፡፡ "ሐጾር ከእነዚህ መንግሥታት ሁሉ ታላቅ ነበረች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያው አነጋገር እና ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚሉትን ይመልከቱ)

በዚያ የሚገኙትን ህይወት ያላቸውን ነገሮች ሁሉ በሰይፍ መቱ… ስለዚህም በህይወት የተረፈ አንዳችም ህይወት ያለው ነገር አልነበረም

እነዚህ ሁለት ሀረጎች ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፤ ሙሉ ለሙሉ ጥፋት መፈጸሙን ያጎላሉ፡፡(ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

እንዲደመሰሱ እርሱ ለይቶ አስቀመጣቸው

"እርሱ" የሚለው ቃል ኢያሱን ያመለክታል፤ ደግሞም እርሱን ራሱን እና ሰራቱን ይወክላል፡፡ በከተማይቱ ውስጥ የሚገኙ ህይወት ያላቸውን ነገሮች ሁሉ ሙሉ ለሙሉ መደምሰስ የሚለው የተነገረው እነዚያ ህይወት ያላቸው ነገሮች ሀሉ ለመጥፋት የተሰጡ እንደሆኑ ተደርጎ ነው፡፡ "ሰራዊቱ ሙሉ ለሙሉ ደመሰሳቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ስኔክቲክ/የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ እና ዘይቤያው አነጋገር የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 11:12

እነርሱን በሰይፍ ስለት መታ

"እነርሱን ገደለ"

በጉብታዎች ላይ የተመሰረቱ ከተሞች

"በትንንሽ ኮረብቶች ላይ የተመሰረቱ ከተሞች"

Joshua 11:14

ለእነርሱ ለራሳቸው

ይህ ሃረግ የሚያመለክተው የእስራኤልን ሰራዊት ነው፡፡ (ደጋጋሚ ተውላጠ ስም/የስም ምትክ)

ሁሉም እስኪሞቱ በሰይፍ ስለት አንድም ሰው ሳይቀር ሁሉንም ገደሉ፡፡ እስትንፋስ ያለውን አንድም ፍጥረት በህይወት አልተዉም፡፡

እነዚህ ሁለት ሀረጎች ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፤ ሙሉ ለሙሉ ጥፋት መፈጸሙን ያጎላሉ፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

ያህዌ ለሙሴ እንዲያደርግ ካዘዘው ውስጥ ሁሉ ሳያደርግ የተወው አንዳች ነገር የለም

ይህ አሉታዊ ሃረግ ኢያሱ ያህዌ ያዘዘውን ሁሉ እንዳደረገ አጉልቶ ይገልጻል፡፡ "ኢያሱ ያህዌ ያዘዘውን ነገር ሁሉ አደረገ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ምፀት/ላይዶክስ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 11:16

ሐላቅ ተራራ… በኣልጋድ

እነዚህ የስፍራ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 11:18

ልባቸውን የጠነከረው ያህዌ ራሱ ነበር

ያህዌ የከተሞቹ ናሪዎች ልባቸው እንዲደነድን ያደረገበት ምክንያት የተገለጸው ልክ ያህዌ ልባቸው ጠንካራ እንዲሆን እንዳደረገ ሆኖ ነው፡፡ "በልበ ደንዳናነት ምላሽ እንዲሰጡ ያደረገው ያህዌ ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 11:21

ዔናቃውያን

እነዚህ የዔናቅ ትውልዶች ነበሩ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ዳቤር…አናብ

እነዚህ የስፍራ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 11:23

ኢያሱ ለእስራኤል ርስት አድርጎ ሰጣት

ኢያሱ ምድሪቱን ለእስራኤላውያን የሰጠበት መንገድ የተገለጸው ለአስራኤላውያን ርስትን በቆሚነት እንደሰጣቸው ተደርጎ ነው፡፡ "ኢያሱ ለእስራኤላውያን ምድሪቱን ቋሚ ርስት አድርጎ ሰጣቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አሁን

ይህ ቃል እዚህ ስፍራ ያገለገለው በዋናው ታሪክ ፍሰት ቆም ለማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ ጸሐፊው የመረጃ ዳራ መስጠት ይጀምራል፡፡ (የመረጃ ዳራ የሚለውን ይመልከቱ)

ንጉሦቹ እነዚህ ናቸው

ይህ እስከ ቁጥር 24 የሚገኙትን የንጉሦች ስም ዝርዝር ያመለክታል፡፡

ዓረባ…አርኖን

እነዚህ የስፍራ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሴዎን… ሔሴቦን

እነዚህን ቃላት በኢያሱ 9፡10 እንዴት እንተረጎሟቸው ይመልከቱ፡፡


Chapter 12

1 የእስራኤልም ሰዎች ድል ያደረጉአቸው ነገሥታት እነዚህ ነበሩ። እስራኤላውያንም ከአዮርዳኖንም ሸለቆ በስተ ምሥራቅ ጀምሮ እስከ ፀሐይ መውጫ ድረስ፥ ከአርሞን ወንዝ ሸለቆ ወደ አርሞንዔም ተራራ ድረስ በምሥራቅ ያለውን ዓረባ ሁሉ ወሰዱ። የአሞራውያን ንጉሥ ሴዎን በሐሴቦን ተቀመጠ። 2 በአርኖንም ሸለቆ አጠገብ ካለችው ከአሮዔር ከሸለቆውም መካከል ጀምሮ የገለዓድን እኩሌታ እስከ ያቦቅ ወንዝ፥ እስከ አሞን ልጆች ዳርቻ ድረስ ገዛ። 3 ሴዎንም በምሥራቅም በኩል ያለውን ዓርባ እስከ ኪኔሬት ባሕር ድረስ፥በቤት የሺሞት መንገድ አጠገብ እስካለው እስከ ዓረባ ባሕር (እስከ ጨው ባሕር) ወደ ምሥራቅ ድረስ በደቡብም በኩል ከፍስጋ ተራራ አፋፍ በታች ያለውን ምድር ገዛ። 4 የባሳን ንጉሥ ዐግ ከራፋይምም ወገን የቀረ፥ በአስታሮትና በኤድራይ ተቀመጠ። 5 እርሱም የአርሞንዔምንም ተራራ፥ ስልካንና ባሳንንም ሁሉ እስከ ጌሹራውያንና እስከ ማዕካታውያን ዳርቻ፥ የገለዓድንም እኩሌታ፥ እስከ ንጉሥ ሀሴቦን ድረስ ገዛው ። 6 የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴና የእስራኤል ልጆች አሸነፉአቸው፤ የእግዚአብሔርም አገልጋይ ሙሴ ርስት አድርጎ ለሮቤል ልጆች፤ ለጋድም ልጆች ለምናሴም ነገድ እኩሌታ ምድሪቱን ሰጣቸው። 7 ኢያሱና የእስራኤል ሕዝብ ያሸነፉአቸ ነገሥታትና አገሮች እነዚህ ናቸው፡- በዮርዳኖስም ማዶ በምዕራብ በኩል፥ በሊባኖስ ሸለቆ አጠገብ ወደ ኤዶን አጠገብ ሃላክ ተራራ ድረስ ነው። ኢያሱም ለእስራኤል ነገዶች ሁሉ ምድሪቱን ርስት አድርጎ ሰጣቸው። 8 ተራራማውን አገር፥ በቆላውንም፥ በዓረባንም፥ የተራሮችን ቁልቁለት፥ ምድረ በዳውንም፥ የደቡቡም ያሉትን ኬጢያውያን፥ አሞራውያንም፥ ከነዓናውያንም፥ ፌርዛውያንም፥ ኤዊያውያንም፥ ኢያቡሳውያንም ሰጣቸው። 9 የኢያሪኮ ንጉሥ ጨምሮ፦ በቤቴል አጠገብ ያለው የጋይ ንጉሥ፥ 10 የኢየሩሳሌም ንጉሥ፥ የኬብሮን ንጉሥ፥ 11 የያርሙት ንጉሥ፥ የለኪሶ ንጉሥ፥ 12 የአግሎን ንጉሥ፥ የጌዝር ንጉሥ፥ 13 የዳቤር ንጉሥ፥ የጌድር ንጉሥ፥ 14 የሔርማ ንጉሥ፥ የዓራድ ንጉሥ፥ 15 የልብና ንጉሥ፥ የአዶላም ንጉሥ፥ 16 የመቄዳ ንጉሥ፥ የቤቴል ንጉሥ፥ 17 የታጱዋ ንጉሥ፥ ይአፌር ንጉሥ፥ 18 የአፌቅ ንጉሥ፥ የሽሮን ንጉሥ፥ 19 የማዶ ንንጉሥ፥የአሶር ንጉሥ፥ 20 የሺምሮን፥ ሚሮን ንጉሥ፥ የአዚፍ ንጉሥ፥ 21 የታዕናክ ንጉሥ፥የመጊዶ ንጉሥ፥ 22 የቃዴስ ንጉሥ፥ በቀርሜሎስ የነበረ የዮቅንዕም ንጉሥ፥ 23 በዶር ኮረብታ የነበረ የዶር ንጉሥ፥ የጌልገላ አሕዛብ ንጉሥ፥ 24 የቲርሳ ንጉሥ፥ ነገሥታቱ ሁሉ ሠላሳ አንድ ናቸው።



Joshua 12:1

አሁን

ይህ ቃል እዚህ ስፍራ ያገለገለው በዋናው ታሪክ ፍሰት ቆም ለማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ ጸሐፊው የመረጃ ዳራ መስጠት ይጀምራል፡፡ (የመረጃ ዳራ የሚለውን ይመልከቱ)

ንጉሦቹ እነዚህ ናቸው

ይህ እስከ ቁጥር 24 የሚገኙትን የንጉሦች ስም ዝርዝር ያመለክታል፡፡

ዓረባ…አርኖን

እነዚህ የስፍራ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሴዎን… ሔሴቦን

እነዚህን ቃላት በኢያሱ 9፡10 እንዴት እንተረጎሟቸው ይመልከቱ፡፡

Joshua 12:6

ሮቤላውያን

እነዚህ የሮቤል ትውልዶች ናቸው፡፡

ጋድአውያን

እነዚህ የጋድ ትውልዶች ናቸው፡፡

የምናሴ ነገድ እኩሌታ

እኩሌታ ነገድ የሚባሉበት ምክንያት ሌላኛው የነገዱ እኩሌታ በከነዓን ምድር ርስታቸውን ስለተቀበሉ ነው፡፡

Joshua 12:7

በኣል ጋድ… ሐላቅ ተራራ…ዓረባ

እነዚህ የስፍራ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 12:9

ጋይ…የርሙት…ለኪሶ…ዔግሎን… ጌድር

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ "የርሙት፣" "ለኪሶ፣" እና "ዔግሎን" የሚሉትን ስሞች በኢያሱ 10፡3 በተረጎሙበት ተመሳሳይ መንገድ ይተርጉሙ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 12:13

ዳቤር…ጌድር…ሔርማ…ዓራድ…ልብና…ዓዶላም…መቄዳ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 12:17

ታጱዋ… ኦፌር… አፌቅ…ለሽሮን… ማዶን… ሐጾር… ሺምሮን ሚሮን… አዚፍ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 12:21

ታዕናክ… መጊዶ…ቃዴስ…ዮቅንዓም…ዶር…ጎይም…ቲርሳ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በድምሩ ሰላሳ አንድ

"በድምሩ 31" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 13

1 ኢያሱም ሸመገለ በዕድሜም አረጀ፤ እግዚአብሔርም አለው፦ አንተ ሸመገልህ፥ በዕድሜህም አረጀህ ያልተወረሰ እጅግ ብዙ ምድር ገና ቀርቶአል። 2 የቀረውም ምድር ይህ ነው፤ የፍልስጥኤማውያንና የጌሹራውያን አገር ሁሉ፥ 3 (በግብፅ ፊት ካለው ከሺሖር ወንዝ ጀምሮ በሰሜን በኩል አስካለው የከነዓናውያን ንብረት ሆኖ ተቆጠረው እስከ አቃሮን ዳርቻ ድረስ፥ የጋዛ፥ የአዛጦን የአስቀሎና፥የጌትና የአቃሮን አምስቱ የፍልስጥኤማውያን መኳንንት።) 4 በደቡብም በኩል የከነዓናውያንም ምድር ሁሉ፥ ለሲዶናውያንም የምትሆን መዓራ እስከ አሞራውያን ዳርቻ እስከ አፌቅ ድረስ፥ 5 የጌባላውያንም ምድር፥ በፀሐይ መውጫ በኩል ሊባኖስ ሁሉ፥ ከኣል ጋድ ከአርሞንዔም ተራራ በታች እስከ ሐማት ድረስ ያለው ። 6 በተራራማውም አገር የሚኖሩትን ሁሉ ከሊባኖስ ጀምሮ እስከ ማሴሮን ድረስ ሲዶናውያን ሁሉ። እነዚህን ከእስራኤል ፊት አባርራቸዋለሁ። እንዳዘዝሁም፤ምድራቸውን ለእስራኤል ርስት አድርገህ ለመመደብ እርግጠኛ ሁን። 7 አሁንም ይህን ምድር ለዘጠኙ ነገድ ለምናሴም ነገድ እኩሌታ ርስት አድርገህ አከፋፍል። 8 የእግዚእብሔር አገልጋይ ሙሴም እንደ ሰጣቸው ከሌላ እኩሌታ የምናሴ ነገድ ጋር የሮብልና የጋድ ሰዎች በምሥራቅ በኩል በዮርዳኖስ ማዶ ሙሴ አዞአቸው የነበረውን ርስታቸውን ተቀበሉ። 9 በአርኖን ወንዝ ሸለቆ ዳር ካለው ከአሮዔር፥ (በሸለቆውም መካከል ካለው ከተማ ጀምሮ) የሜድባን ሜዳ ሁሉ እስከ ዲቦን ድረስ፥ 10 በሐሴቦንም የአሞርውያን ንጉሥ የሴዎን ከተሞች ሁሉ እስከ አሞራውያን ዳርቻ ድረስ፥ 11 ገለዓድንም፥ የጌሹራውያንና የማዕካታውያንን አካባቢ ሁሉ፥ የአርሞንዔምንም ተራራ ሁሉ፥ባሳንንም ሁሉ እስከ ሰልካ ድረስ፥ 12 በባሳን የነበረውን በአስታሮትና በኤድራይ የነገሠውን የዐግን መንግሥት ሁሉ፥ እነርሱም ከራፋይም የቀረ ነበረ፤ እነዚህንም ሙሴ መታቸው አወጣቸውም። 13 ነገር ግን የእስራኤል ሰዎች ጌሹራውያንን ወይም ማዕካታውያንን አላወጡም ነበር። በዚህ ፈንታ ጌሹርና ማዕካት እስከ ዛሬም ድረስ በእስራኤል መካከል ይኖራሉ። 14 ሙሴም ለሌዊ ነገድ ለብቻ ርስት አልሰጠም። እግዚአብሔር ለሙሴ እንደ ተናገረው ለእስራኤል አምላክ ለእግዚአብሔር የሚቀረበው፥ በእሳት የተደረገ መሥዋዕት ርስታቸው ነው። 15 ሙሴም ለሮቤል ልጆች ነገድ በየወገናቸው ርስትን ሰጥጣቸው። 16 ድንበራቸውም በአርኖን ሸለቆ ዳር ካለችው ከአሮዔር ጀሞሮ በሸለቆው መካከል ያለችው ከተማ፥ 17 ሐሴቦንና በሜዳውም ያሉት ከተሞችዋ ሁሉ፥ዲቦን፥ ባሞት በኣል፥ ቤት በኣልምዖን፥ 18 ያሀጽና ቅዴሞት፥ ሜፍዓት፥ 19 ቂርያታይም፥ ሴባማ፥ ጼሬትሻሐና በሸለቆውም ተራራ ያለውና ሁሉ ሮቢን ተቀበለ። 20 ሮቤም ቤተ ፌጎርን፥ ከፈስጋ ተራራ በታች ያለው ምድርን፥ ቤት የሺሞትን፥ 21 የሜዳውም ከተሞች ሁሉ፥ የአሞራውያን ንጉሥ የሴዎን መንግሥት፥ በሐሴቦንም የነገሠው፥ ሙሴም እርሱንና በምድሪቱ የተቀመጡትን የምድያምን አለቆች፥ ኤዊን፥ ሮቆምን፥ ሱርን፥ ሑርንና ሪባን፥ የሴዎን መሳፍንት፥ መታቸው። 22 የእስራኤል ሰዎች ከገደሉአቸውም ሰዎች ጋር ምዋርተኛውን የቢዖርን ልጅ በለዓምን በሰይፍ ገደሉ። የሮቤልም ልጆች ድንበር የዮርዳኖስ ወንዝና ዳርቻው ነበረ። 23 የሮቤል ነገድ ድንበር የዮርዳኖስ ወንዝ ነው፥ ይህም ድንበራቸው ነው። ይህም ከከተሞቻቸውና መንደሮቻቸው በየወገኖቻቸው ለሮቤል ነገድ የተሰጣቸው ርስት ነበረ። 24 ይህም መሴ ለጋድ ነገድ በየውገኖቻቸው ርስት አድርጎ የሰጣቸው ነው። 25 ድንበራቸውም ኢያዜርና የገለዓድ ከተሞች ሁሉ፥ የአሞራውያንም ምድር እኩሌታ፥ 26 ከረባት በስተምሥራቅ፥ አስካለው እስከ አሮዔር ድረስ፥ ከሐሴቦን ጀምሮ እስከ ራማት ምጽጴ፥ እስከ ብጦኒም ድረስ፥ ከመሃናይም ጀምሮ እስከ ዳቤር ዳርቻ ድረስ ነበር። 27 ሙሴም ቤትሀራምን፥ ቤትኒምራ፥ ሱኮትና ጻፎን፥ የቀሩትንም የሐሴቦን ንጉሥ የሴዎን መንግሥት ከዮርዳኖስን እንደ ድንበር በምሥራቅ በኩል ባለው በዩርዳኖስ ማዶ የኪኔሬት ባሕር ወዲያኛው ዳርቻ ሰጣቸው። 28 ይህም የጋድ ነገድ ከከተሞቻቸውና ከመንደሮቻቸው ጋር በየወገኖቻቸው ርስት ነበረ። 29 ሙሴም ለምናሴ እኩሌታ ነገድ ርስትን ሰጣቸው። ለምናሴም ነገድ እኩሌታ በየወገኖቻቸው መሠረት የተመመደበ ነበረ። 30 ድንበራቸውም ባሳን ሁሉ፥ ከመሃናይም ጀምሮ የባሳን ንጉሥ የዐግ መንግሥት፥ በባሳንም ያሉት የኢያፅር መንደሮች ሁሉ ስድሳው ከተሞች፤ 31 የገለዓድም እኩሌታ፥ አስታሮትና ኤድራይ ነበር፤ (የ'ዐግ በባሳን ያሉ የመንግሥት ከተሞች) ። እነዚህም ለምናሴ ልጅ ለማኪር ልጆች ሆኑ፤ ለማኪር ሰዎች እኩሌታ በየወገኖቻቸው ይህ ነበረ። 32 ይህም ሙሴ በምሥራቅ በኩል በኢያሪኮ አንጻር በዮርዳኖስ ማዶ በሞዓብ ሜዳ ሳለ፥ የከፈለው ርስት ነው። 33 ሙሴም ለሌዊ ነገድ ርስት አልሰጣም ነበር። የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንደ ተናገራቸው ርስታቸው ነው።



Joshua 13:2

አስከ አሁን ገና የቀረው ምድር ይህ ነው

እስራኤል ገና ሊይዘው የሚገባው ምድር ይህ ነው በማለት ማብራራት ይቻላል፡፡ "አስራኤላያን ገና ወዲፊት የሚይዙት ምድር ይህ ነው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ሺሖር

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የከነዓናውያን ንብረት ነው ተብሎ የሚቆጠር

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "አሁን ከነዓናውያን ንብረታቸው አድርው የሚቆጥሩት" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ኤዋውያን

ይህ የአንድ ቡድን ሰዎች የወል ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:4

ዓራ…አፌቅ…በኣልጋድ…ኤርሞንዔም ተራራ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ጌባላውያን

ይህ በገባኦን የሚኖሩ ሰዎች የወል ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:6

ማሴሮን

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ምድር…እርስት አድርጎ

እስራኤላውያን የእኔ ነው የሚሉት ምድር ቋሚ ሃብቸው አድርገው እንደሚቀበሉት ርስታቸው ተድረጎ ተገልጽዋል፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:8

አርኖን… ሜድባ… ዲቦን

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሸለቆ

ወንዙ ከጎንና ጎኑ ከሚገኘው ስፍራ እጅግ ዝቅ ብሎ የሚገኝበት ነው

አንባ

ከወንዝ በላይ ከፍ ብሎ የሚገኝ ሜዳማ መሬት

Joshua 13:10

ሔሴቦን… ሰልካ… አስታሮት… ኤድራይ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የጌሹራውያን እና ማዕካታውያን ግዛት

" የጌሹራውያን እና ማዕካታውያን የሚኖሩበት ምድር"

ማዕካታውያን… ራፋይም

እነዚህ የህዝብ የወል ስም ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሙሴ መታቸው

እዚህ ስፍራ "ሙሴ" የሚወክለው ራሱን እና እርሱ የሚመራቸውን እስራኤላውያን ሰራዊት ነው፡፡ "ሙሴ አና እስራኤላውያን መቷቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚለውን ይመልቱ)

Joshua 13:13

ጌሹራውያን ወይም ማዕካታውያን

ይህ የአንድ ቡድን ሰዎች የወል ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ጌሹራውያን እና ማዕካታውያን በእስራኤላውያን መሃል ይኖራሉ

"ጌሹራውያን" እና "ማዕካታውያን" አንድም "የጌሹራውያን" እና "የማዕካታውያን" አባቶች ናቸው ወይም የሚኖሩባቸው ከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ "እነዚያ ህዝቦች በእስራኤላውያን መሃል ይኖራሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ ዛሬ ድረስ

ይህ ጸሐፊው ይህንን መጽሐፍ እሰከ ጻፈበት ጊዜ ድረስ ያለውን ጊዜ ያመለክታል

Joshua 13:14

ሙሴ ምንም ርስት አልሰጣቸውም

ሙሴ ለእስራኤል ነገድ የሰጠው ምድር ቋሚ ሃብት እንደተቀበሉ ተደርጎ ተገልጽዋል፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

ለያህዌ የሚቀርቡ መሥዋዕቶቸ … ርስታቸው ነው

ጸሐፊው ሌዋውያን በክህነት ያህዌን በማገልገል ያላቸውን ታላቅ ክብር መስዋዕቶቹን እነርሱ እንደሚወርሷቸው ነገሮች አድርጎ ይገልጻል፡፡ "ለያህዌ የሚቀርቡ መሥዋዕቶቸ … ለእነርሱ የሚሰጣቸው ይሆናል" (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:15

አርኖን… ሜድባ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሸለቆ… አንባ

x

Joshua 13:17

ሔሴቦን… ዲቦን… ባሞትበኣል… ቤትበኣልምዖን… ያሀጽ… ቅዴሞት… ሜፍዓት… ቂርያታይም… ሴባማ… ጼሬትሻሐር

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:20

ቤት ፌጎር… ፊስጋ… ቤት የሺሞት… ሐሴቦን

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሴዎን… ኤዊ… ሮቆም… ሱር… ሑር… ሪባ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ከምድያም መሪዎች ጋር

"የምድያም መሪዎችን እንዳሸነፈ"

Joshua 13:22

ይህ ድንበራቸው ነው

የዮርዳኖስ ወንዝ የሮቤል ነገድ የተቀበለው ምዕራባዊ ዳርቻ ነው

ይህ የሮቤል ነገድ ርስት ነበር

ሙሴ ለሮቤል ነገድ የሰጠው ምድር የሮቤል ነገድ በቋሚነት እንደ ተቀበለው ርስት ተደርጎ ይገለጻል፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

ለእያንዳንዱ ጎሳቸው ተሰጠ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ሙሴ ለእያንዳንዱ ጎሳቸው የሰጠው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:24

ኢያዜር…አሮዔር… ሐሴቦን… ራማት ምጽጴ.. ብጦኒም… መሃናይም… ዳቤር

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:27

ቤት ሀራም… ቤት ኒምራ… ጻፎን… ሐሴቦን

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ የጋድ ነገድ ርስት ነው

ሙሴ ለጋድ ነገድ የሰጠው ምድር የጋድ ነገድ በቋሚነት እንደ ተቀበለው ርስት ተደርጎ ይገለጻል፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:29

ሙሴ ለምናሴ ነገድ እኩሌታ ርስት ሰጠ

ሙሴ ለምናሴ ነገድ እኩሌታ የሰጠው ርስት ለእነርሱ እንደ ሰጠው ቋሚ ርስት ተደርጎ ተገልጽዋል፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

የምናሴ ነገድ እኩሌታ

የነገዱ እኩሌታ ብቻ ይህንን ምድር ተቀብሏል፣ ምክንያቱ የነገዱ ቀሪው እኩሌታ ከዮርዳኖስ ማዶ ባለው ምድር ርስቱን ተቀብሏል፡፡

ተሰጥቷቸው ነበር

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ሙሴ ርስታቸውን ሰጥቷቸው ነበር" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

መሃናይም… ኢያዕር… አስታሮት… ኤድራይ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የተሰጡት እነዚህ ነበሩ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ሙሴ እነዚህን ሰጠ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ማኪር

ይህ የወንድ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 13:32

ሙሴ የሰጣቸው ርስት ይህ ነው

ሙሴ ለእስራኤል ነገዶች የሰጣቸው ከዮርዳኖስ በስተምስራቅ የሚገኘው ምድር በቋሚነት እንደሰጣቸው ርስት ተደረጎ ተገልጽዋል፡፡ "ይህ ሙሴ ለእነርሱ ርስት አድርጎ የሰጣቸው ምድር ነው፡፡" (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

የእስራኤል አምላክ ያህዌ፣ የእነርሱ ርስት ነው

ጸሐፊው ሌዋውያን በክህነት አገልግሎታቸው ያህዌን በማገልገል ያላቸውን ታላቅ ክብር የገለጸው የሚወርሱት ያህዌን እንደሆነ በመናገር ነው፡፡ "የእነርሱ ርስት የእስራኤል አምላክ ያህዌ ነው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 14

1 የእስራኤልም ሕዝብ በካነዓን ምድር የወረሱት ካህኑ አልዓዛርና የነዌ ልጅ ኢያሱ በእስራኤልም ነገድ መካከል የአባቶቻቸው አለቆች ያካፈሉአቸው ርስት ይህ ነው፤ 2 እግዚአብሔር በሙሴ እጅ እንዳዘዘ ለዘጠኙ ነገዶችና ለእኩሌታው በየርስታቸው በዕጣ አካፈሉአቸው፤ 3 ለሁለቱ ነገድና ለእኩሌታው ነገድ በዮዳኖስ ማዶ ሙሴ ርስት ሰጥቶ ነበር፤ ነገር ግን በመካከላቸው ለሌዋውያን ርስት አልሰጣቸውም። 4 የዮሴፍ ነገድ፥ ምናሴና ኤፍሬም ሁለት ነገዶች ነበሩ። ለሌዋውያንም ከሚቀመጡባቸው ከተወሰኑ ከተሞች፥ ለእንስሶቻቸውና ለከብቶቻቸውም ከሚሆን መሰምርያቸው በቀር በምድሩ ውስጥ ድርሻ አልሰጡአቸውም። 5 እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘው የእስራኤል ሕዝብ አደረጉ፥ ምድሩንም ተካፈሉ። 6 የይሁዳም ነገድ በጌልገላ ወደ ኢያሱ ቀረቡ። ቄኔዛዊውም የዮፎኒ ልጅ ካሌብ እንዲህ አለው፦ ለእግዚአብሔር ሰው ለሙሴ ስለ እኔና ስለ አንተ እግዚአብሔር በቃዴስ በርኔ የተናገረውን ነገር ታውቃለህ። 7 የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ ምድርን እሰልል ዘንድ ከቃዴስ በርኔ በላከኝ ጊዜ እኔ የአርባ ዓመት ሰው ነበርሁ፤ እኔም በልቤ እንደ ነበረ መረጃ አመጠሁለት። 8 ነገር ግን ከእኔ ጋር የሄዱ ወንድሞቼ የሕዝቡን ልብ በፍርሃት አቀለጡ። እኔ ግን አምላኬን እግዚአብሔርን ፈጽሜ ተከተልሁ። 9 ሙሴም በዚያ ቀን፦ አምላኬን እግዚአብሔርን ፈጽመህ ተከትለሃልና እግርህ የረገጠው ምድር ለአንተና ለልጆችህ ለዘላለም በእርግጥ ርስት ይሆናል ብሎ ማለ። 10 አሁንም፥ እነሆ፥ እግዚአብሔር ለሙሴ ይህን ቃል ከተናገር በኋላ፥ እስራኤል በምድረ በዳ ሲጓዙ፥ እርሱ እንደ ተናገረኝ እግዚአብሔር እነዚህን አርባ አምስት ዓመት በሕይወት አኖረኝ። እነሆ፥ ለእኔ ዛሬ ሰማንያ አምስት ዓመት ሆነኝ። 11 ሙሴም በላከኝ ጊዜ እንደ ነበርሁ፥ ዛሬ ጉልበታም ነኝ፥ ጉልበቴም በዚያን ጊዜ እንደ ነበር፥ እንዲሁ ዛሬ ለመዋጋት፥ ለመውጣትና ለመግባትም ጉልበቴ ያው ነው። 12 እንግዲህ በዚያን ቀን እግዚአብሔር የተናገረውን ይህን ተራራማ አገር ስጠኝ። አንተም በዚያ ቀን ታላላቅና በተመሸጉ ከተሞቻቸው ጋር ዔናቃውያን በዚያ እንደ ነበሩ ሰምተህ ነበር። እግዚአብሔርም እንደ ተናገረ እግዚአብሔርም ከእኔ ጋር ይሆናል፥ አሳድዳቸዋለሁ። 13 ኢያሱም ባረከው፤ ለዮፎኒም ልጅ ለካሌብ ኬብሮንን ርስት አድርጎ ሰጠው። 14 ስለዚህም የእስራኤልን አምላክ እግዚአብሔርን ፈጽሞ ስለ ተከተለ ኬብሮን እስከ ዛሬ ለቄኔዛዊው ለዮፎኒ ልጅ ለካሌብ ርስት ሆንች። 15 የኬብሮንም ስም አስቀድሞ ቂርያት አርባቅ ትባል ነበር። (አርባቅም በዔናቅ ሰዎች መካከል ከፍ ያለ ነበረ።) ምድሪቱም ከጦርነት ዐረፈች።



Joshua 14:1

የእስራኤል ህዝብ ርስት አድርጎ የተቀበላቸው ስፍራዎች

የእስራኤል ህዝብ ያገኘው ምድር የተገለጸው በቋሚነት እንደተቀበለው ሃብቱ ተደርጎ ነው፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

የነገድ አለቆች

"የነገዶቹ አለቆች"

Joshua 14:2

ርስታቸው የተከመረጠላቸው በእጣ ነበር

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "አልዓዛር፣ ኢያሱ፣ እና የጎሳ አለቆች ርስታቸውን ለማከፋፈል እጣ ጣሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

በሙሴ እጅ

እዚህ ስፍራ"እጅ" የሚለው ሙሴን ራሱን እና ያህዌ ሙሴን የእርሱን ትዕዛዝ ማስፈጸሚያ አድርጎ እንደ ተገለገለበት የሚገልተጽ ቃል ነው፡፡ "በሙሴ አማካይነት" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚለውን ይመልቱ)

ሙሴ የሁለቱን ነገዶች እና የአንዱን ነገድ እኩሌታ ርስት ከዮርዳኖስ ባሻገር ሰጠ፣ ለሌዋውያን ግን ምንም ርስት አልሰጣቸውም

ሙሴ ለነገዶቹ የሰጣቸው መሬት የተገለጸው በቋሚነት እንደ ተቀበሉት ርስት ተደርጎ ነው፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

ሌዋውያን ከምድሪቱ ርስት ተደርጎ ምንም ደርሻ አልተሰጣቸውም

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ሙሴ ለሌዋውያን ምንም ድርሻ ርስት አድርጎ አልሰጣቸውም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ድርሻ

"ክፍል"

ነገር ግን አንዳንድ ከተሞች ብቻ ለመኖሪያነት

ግሱ የተወሰደው ከቀደመው ሀረግ ነው፡፡ "ነገር ግን እርሱ ለመኖሪያነት አንዳንድ ከተሞችን ብቻ ሰጣቸው" (ኢሊፕሲስ/የተተወ/የተዘለለ የሚለውን ይመልከቱ)

የግጦሽ መሬት

ለብቶች ግጦሽ የሚውል መስክ

ቁሳዊ ሃብት

ለቤተሰቦቻቸው ያቀርቧቸው ዘንድ የሚያስፈልጋቸው ቁሳዊ/አካላዊ ነገሮች

Joshua 14:6

ዮፎኒ

ይህ የወንድ ስም ነው (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ቄኔዛዊ

ይህ የአንድ ቡድን ሰዎች የወል ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእርሱ ዳግም በልቤ ማድረግ እንዳሰብኩት መረጃ ይዤ መጣሁ

እዚህ ስፍራ "ልብ" የሚለው ቃል የሚወክለው ሃሳብን ነው፡፡ ሀረጉ ፈሊጣው ሲሆን የሚያመለክተው በእውነተኛነት የቀረበን መረጃ ነው፡፡ "ለእርሱ ዳግም እውነተኛ መረጃ ይዤ መጣሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የህዝቡ ልብ በፍርሃት እንዲቀልጥ አደረጉ

ህዝቡ በጣም እንዲፈራ ማድረግ የተገለጸው የህዝቡ ልብ እንዲቀልጥ እንደተረገ ተደርጎ ነው፡፡ "ህዝቡ በጣም እንዲፈራ አደረጉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እኔ ሙሉ ለሙሉ ያህዌን ተከተልኩ

ለያህዌ ታማኝ መሆን የተገለጸው ያህዌን ሙሉ ለሙሉ እንደ መከተል ተደርጎ ነው፡፡ "ሁሌም ለያህዌ ታማኝ ነበርኩ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሪቱ… ለአንተ እና ለልጆችህ ለዘለዓለም ርስት ትሆናለች

ካሌብ እና የእርሱ ትውልድ የሚኖራቸው ምድር የተገለጸው በቋሚነት እንደ ተቀበሉት ርስት ተደርጎ ነው፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

እግርህ የረገጠውን ምድር

እዚህ ስፍራ "እግርህ" የሚለው የሚወክለው ካሌብን ነው፡፡ "የረገጥከው ምድር" (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚለውን ይመልቱ)

Joshua 14:8

የህዝቡ ልብ በፍርሃት እንዲቀልጥ አደረጉ

ህዝቡ በጣም እንዲፈራ ማድረግ የተገለጸው የህዝቡ ልብ እንዲቀልጥ እንደተረገ ተደርጎ ነው፡፡ "ህዝቡ በጣም እንዲፈራ አደረጉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እኔ ሙሉ ለሙሉ ያህዌን ተከተልኩ

ለያህዌ ታማኝ መሆን የተገለጸው ያህዌን ሙሉ ለሙሉ እንደ መከተል ተደርጎ ነው፡፡ "ሁሌም ለያህዌ ታማኝ ነበርኩ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሪቱ… ለአንተ እና ለልጆችህ ለዘለዓለም ርስት ትሆናለች

ካሌብ እና የእርሱ ትውልድ የሚኖራቸው ምድር የተገለጸው በቋሚነት እንደ ተቀበሉት ርስት ተደርጎ ነው፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

እግርህ የረገጠውን ምድር

እዚህ ስፍራ "እግርህ" የሚለው የሚወክለው ካሌብን ነው፡፡ "የረገጥከው ምድር" (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚለውን ይመልቱ)

Joshua 14:10

ተመልከት

"ትኩረት ስጥ፣ ምክንያቱም የምናገረው እውነትም ዋጋ ያለውም ነገር ነው"

እስራኤል በምድረ በዳ ሲጓዝ

"የእስራኤል ህዝብ በምድረ በዳ ሲጓዝ"

አሁንም ጥንካሬዬ በዚያን ጊዜ እንደነበረው ነው

"በዚያን ጊዜ ጠንካራ የነበርኩትን ያህል አሁንም ጠንካራ ነኝ"

ስገባና ስወጣ

ይህ የየዕለት ክንዋኔን የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡ "በየዕለቱ ለማደርጋቸው ነገሮች" (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 14:12

ተራራማ አገር

ሊሰጡ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ብዙ ትላልቅ ኮረብቶች ወይም ትናንሽ ተራሮች 2) አንድ ተራራ

ዔናቅ

ይህ የአንድ ቡድን ሰዎች የወል ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 14:13

ኬብሮንን ለካሌብ ርስት አድርገህ ሰጠው

ኬብሮን ካሌብ በቋሚነት እንደተቀባለት ርስት ተደርጋ ተገልጻለች፡፡ (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ ዛሬ ድረስ

ይህ ጸሐፊው ይህንን መጽሐፍ እሰከ ጻፈበት ጊዜ ድረስ ያለውን ጊዜ ያመለክታል፡፡

እርሱ ሙሉ ለሙሉ ያህዌን ተከትሏል

ለያህዌ ታማኝ መሆን የተገለጸው ሙሉ ለሙሉ ያህዌን መከተል ተደርጎ ነው፡፡ "ሁሌም ለያህዌ ታማኝ ነበር" (ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)

ቂርያት አርባቅ

ይህ የስፍራ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ከዚህ በኋላ ምድሪቱ ከጦርነት አረፈች

ህዝቡ ከዚያ በኋላ ጦርነት ውስጥ አለመግባቱ የተገለጸው ምድሪቱ ራሷ ሰው እንደሆነች እና ከጦርነት እንዳረፈች ተደርጎ ነው፡፡ ይህንን ሀረግ በኢያሱ 11፡23 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ "ከዚህ በኋላ ህዝቡ በምድሪቱ ጦርነት አላደረገም" (ሰውኛ ዘይቤ እና ዘይቤያው አነጋር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 15

1 ለይሁዳም ልጆች ነገድ በየወገናቸው መሬትን ማከፋፈል እስከ ጺን ምድረ በዳ እስከ ደቡብም መጨረሻ እስከ ኤዶምያስ ዳርቻ ድረስ ዕጣ ሆነላቸው። 2 በደቡብም በኩል ያለው ድንበራቸው እስከ ጨው ባሕር መጨረሻ ወደ ደቡብ እስከሚያይ እስከ ባሕረ ልሳን ነበረ። 3 ከዚያም ቀጥሎ ከኮረብታ በስተደቡብ በኩል ወደ ጺንም አለፈ፤በቃዴስ በርኔ ወደ ደቡብ በኩል ይዘልቃል፤ በሐጽሮንም በኩል አልፎ ወደ አዳርም ደረሰ፥ ወደ ቀርቃ ዞረ፥ 4 ወደ አጽሞንም አለፈ፥ በግብፅም ወንዝ በኩል ወጣ፥ የድንባሩም መውጫ በባሕሩ አጠገብ ነበር፤ በደቡብ በኩል ያለው ድንበራቸው ይህ ነው። 5 በምሥራቅም በኩል ያለው ድንበር እስከ ጨው ባሕር እስከ ዮርዳኖስም መጨረሻ ነበረ። በሰሜንም በኩል ያለው ድንበር በዩርዳኖስ መጨረሻ እስካለው እስከ ባሕሩ ልሳን ድረስ ነበር። 6 ከዚያም ድንበሩ ወደ ቤት ሖግላ ወጣ፥ በቤት ዓርባ በሰሜን በኩል አለፈ። (ወደ ሮቤልም ልጅ ወደ ቦሀን) ድንጋይ ወጣ። 7 ድንበሩም ከአኮር ሸለቆ ወደ ዳቤር ወጣ፥ በሰሜን በኩል በአዱሚም ኮረብታ ፊት ለፊት፥በወንዙም በደቡብ በኩል ወዳለችው ወደ ጌልገላ ዞረ። ከዚያም ድንበሩ ወደ ቤት ሳሚስ ውኃ አለፈ፥ መውጫውም በዓይን ሮጌል አጠገብ ነበረ። 8 ከዚያ ድንበሩም በሄኖም ልጅ ሸለቆ አጠገብ (ኢየሩሳሌም) ወደምትባለው ወደ ኢያቡሳዊው ወደ ደቡብ ወገን ወጣ፤ ድንበሩም በራፋይም ሸለቆ ዳር በሰሜን በኩል ባለው በሄኖም ሸለቆ ፊት ለፊት በምዕራብ ወገን ወዳለው ተራራ ራስ ላይ ወጣ። 9 ድንበሩም ከተራራው ራስ ወደ ኔፍቶ ውኃ ምንጭ ደረሰ፥ ወደ ዔፍሮንም ተራራ ከተሞች ወጣ። ቂርያትይዓሪም ወደምትበል ወደ በኣላ ደረሰ። (ከዚያም ድንበሩ በባኣላ ዙሪያ እንደ ቂርያት በተመሳሳይ ታጠፈ) ። 10 ድንበሩም ከባአላ በምዕራብ በኩል ወደ ሴይር ተራራ ዞረ፤ክሳሎን ወደምትባል ወደ ይዓሪም ተራራ ወገን በሰሜን በኩል አለፈ፤ ወደ ቤት ሳሚስ ወረድ፥ በተምና በኩልም አለፈ። 11 ድንበሩም ወደ አቃሮን ወደ ሰሜን ወገን ወጣ፤ወደ ሽክሮን ደረሰ ወደ በኣላ ተራራ አለፈ፥ በየብኒኤል በኩልም ወጣ፤ የድንበሩም መውጫ በባሕሩ አጠገብ ነበረ። 12 በምዕራቡም በኩል ያለው ድንበር እስከ ታላቁ ባሕርና እስከ ዳርቻው ድረስ ነበረ።ለይሁዳ ልጆች በየወገናቸው በዙሪያው ያለ ድንበራቸው ይህ ነው። 13 እግዚአብሔርም ኢያሱን እንዳዘዘው ለዮፎኒ ልጅ ካሌብ በይሁዳ ልጆች መካከል ቂርያት አርበቅ የምትባለውን ከተማ ድርሻ አድርጎ ሰጠው፤ እርስዋም ኬብሮን ናት፥ ይህም ዘርባቅ የዔናቅ አባት ነበረ። 14 ካሌብም ሦስቱን የዔናቅን ልጆች ሴስን፥ አኪመንንና ተላሚን ከዚያ አሳደደ። 15 ከዚምም በዳቤር ሰዎች ላይ ወጣ፤ የዳቤርም ስም አስቀድሞ ቂርያት ሤፍር ትባል ነበር። 16 ካሌብም እንዲህ አለ፦ ቂርያት ሤፍርን ለሚመታ ለሚይዛትም ልጄን ዓክሳን አጋባዋለሁ አለ። 17 የካሌብ ወንድም የቄኔዝ ልጅ ጎቶንያል ያዛት። ስለዚህም ካሌብ ልጁን ዓክሳን አጋባው። 18 ዓክሳም ወደ እርሱ በመጣች ጊዜ ከአባትዋ እርሻ ለመለምን ገፋፈችው፤ እርስዋም ከአህያዋ ወረደች፤ካሌብም፦ ምን ፈለግሽ? አላት። 19 እርስዋም፦ ስጦታ ስጠኝ፤ የኔጌቭ ምድር ሰጥተኸኛል፥ አሁን ደግሞ የውኃውን ምንጭ ስጠኝ አለችው። እርሱም የላይኛውንና የታችኛውን ምንጭ ሰጣት። 20 በየወገኖቻቸውም የይሁዳ ልጆች ነገድ የተሰጠ ርስት ይህ ነው። 21 በድቡብም በኩል በምድራቸው ዳርቻ አጠገብ እስከ ኤዶምያስ ድንበር ያሉትን የይሁዳ ልጆች ነገድ ከተሞች እነዚህ ነበሩ ቀብስኤል፥ ዓዴር፥ ያጉር፥ 22 ቂና፥ ዲሞና፥ ዓድዓዳ፥ 23 ቃዴስ፥ ሐጾር፥ ዪትናን 24 ዚፍ፥ጠሌም፥በዓሎት። 25 ሐጾርሐ ዳታ፥ ሐጾር የምትባለውም ቂርታይሐጾር፥ 26 አማም ሽማዕ፥ ሞላዳ፥ 27 ሐጸርጋዳ፥ሐሽሞን፥ ቤትጳሌጥ፥ 28 ሐጸርሹዓል፥ ቤርሳቤህ፥ ቢዝዮትያ፥ 29 በኣላ፥ ዒዮም፥ ዓጼም፥ 30 ኤልቶላድ፥ ኪሲል፥ ሔርማ፥ 31 ጺቅላግ፥ ማድማና፥ ሳንሳና፥ 32 ልባዎት፥ ሺልሂም፥ ዓይን፥ ሪሞም፤ ሀያ ዘጠኝ ከተሞችና መንደሮቻቸው። 33 በቆላው ኤሽታኦል፥ ጾርዓ፥ አሽና፥ 34 ዛኖዋ፥ ጫይንገኒም፥ ያጱዋ፥ ዓይናም፥ 35 የሩት፥ ዓዶላም፥ ሰኮት፥ ዓዜቃ፥ 36 ሽዓራይም፥ ዓዲታይም፥ ግርራ፥ ግርሮታይም፤ አሥራ አራት ከተሞችና መንደሮቻቸው። 37 ጽናን፥ ሐዳሻ፥ ሚግዳልጋድ፥ 38 ዲልዓን፥ ምጽጳ፥ ዮቅትኤል፥ 39 ለኪሶ፥ በጽቃት፥ አግሎን 40 አዶላም፥ ከቦን፥ ለሕማስ፥ ኪትሊሽ፥ 41 ግዴሮት፥ ቤት ዳጎን፥ ናዕማ፥ መቄዳ፤አሥራ ስድስት ከተሞችና ቁጥር ስፍር የሌላቸው መንደሮቻቸው። 42 ልብና፥ ዔቴር፥ ዓሻን፥ 43 ይፍታሕ፥ አሽና፥ንጺብ፥ 44 ቅዒላ፥ አክዚብ፥ መሪሳ፤ ዘጠኝ ከተሞችና ቁጥር ስፍር የሌላቸው መንደሮቻቸው። 45 አቃሮን፥ ከተመሸጉና ካልተመሸጉ ከተሞችና መንደሮችዋ ጋር፤ 46 ከአቃሮንም ጀምሮ እስከ ባሕር ድረስ በአዛጦን አጠገብ ያሉት ሁሉ ከመንደሮቻቸው ጋር። 47 በአዛጦን የተመሸጉና መንደሮችዋም፥ ጋዛና የተመሸጉ ከተሞችና መንደሮችዋ፥ እስከ ግብፅ ወንዝና እስከ ታላቁ ባሕር ካርቻ ክረስ። 48 በተራራማውም አገር ሳምር፥ የቲር፥ ሶኮ፥ 49 ደና፥ ዳቤር የምትባለው ቂርያትሰና፥ 50 ዓባብ፥ኤሽትሞዓ፥ ዓኒም፥ 51 ጎሶም፥ ሖሎን፥ ጊሎ፤ አሥራ አንድ ከተሞችና ቁጥር ስፍር የሌላቸው መንደሮቻቸው። 52 አራብ፥ ዱማ፥ ኤሽዓን፥ 53 ያንም፥ ቤትታጱዋ፥ አፌቃ፥ 54 ሑምጣ፥ ኬብሮን የምትባል ቂርያትአርባቅ፥ ጺዖር ፤ ዘጠኝ ከተሞችና ቁጥር ስፍር የሌላቸው መንደሮቻቸው። 55 ማዖን፥ ቀርሜሎስ፥ ዚፍ፥ ዩጣም 56 ኢይዝራሴል፥ ዮቅድዓም፥ ዛኖዋሕ፥ 57 ቃይን፥ ጊብዓ፥ ተምና፤ አሥር ከተሞና ቁጥር ስፍር የሌላቸው መንደሮቻቸው። 58 ሐልሑል፥ ቤት ጹር፥ ጌዶር፥ 59 ማዕራት፥ ቤትዓኖት፥ ኤልትቆን፤ስድስት ከተሞችና ቁጥር ስፍር የሌላቸው መንደሮቻቸው። 60 ቂርያትይዓሪም የምትባለው ቂርያት በኣል፥ ረባት፤ ሁለት ከተሞችና መንደሮቻቸው። 61 በምድረ በዳ ቤትዓረባ፥ ሚዲን፥ ስካካ፥ 62 ኒብሻን፥ የጨው ከተማ፥ ዓይንጋዲ፤ ስድስት ከተሞችና ቁጥር ስፍር የሌላቸው መንደሮቻቸው። 63 በኢየሩሳሌም የተቀመጡትን ኢያቡሳውያንን ግን የይሁዳ ልጆች ሊያሳድዱአቸው አልተቻላቸውም፤ ኢያቡሳውያንም እስከ ዛሬ በይሁዳ ልጆች መካከል በኢየሩሳሌም ውስጥ ተቀምጠዋል።



Joshua 15:1

ጺን

ይህ በረሃማ ስፍራ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ከጨው ባህር መጨረሻ ፣ ፊቱን ወደ ደቡብ ከመለሰው ባህረ ሰላጤ

" ወደ ደቡብ ፊቱን ከመለሰው ባህረ ሰላጤ፣ በጨው ባህር መጨረሻ" እነዚህ ሁለት ሀረጎች ተመሳሳይ አቅጣጫን ያመለክታሉ፡፡ ሁለተኛው ሀረግ ደቡባዊው ዳርቻ የሚጀምርበትን ነጥብ ያብራራል

ወደ ደቡብ ፊቱን ከመለሰው ባህረ ሰላጤ

"እስከ ደቡብ ከሚደርሰው ባህረ ሰላጤ" ወይም "ከደቡባዊ ባህረ ሰላጤ"

ባህረ ሰላጤ

ወደ መሬት ክፍል ገባ የሚል አነስተኛ የባህር ክፍል

Joshua 15:3

ድንበራቸው

"የይሁዳ ነገድ ድንበር የሆነ ምድር"

አቅረቢም…ጺን… ሐጽሮን… አዳር… ቀርቃ… አጽሞን

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የግብጽ ጅረት

በግብጽ አጠገብ፣ በምድሪቱ ደቡባዊ ምዕራብ ዳርቻ የሚገኝ ትንሽ የወንዝ ውሃ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:5

ዮርዳኖስ ወንዝ በሚገባበት

ወንዙ ወደ ባህሩ ገብቶ የሚያበቃበት ነጥብ የወንዙ መግቢያ ተብሎ ይገለጻል፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ዳርቻ… መውረጃ

"ዳርቻ… ነበር"

ቤት ሖግላ… ቤት ዓረባ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የቦሀን ድንጋይ

ይህ ምናልባት አንድ ሰው ለድንበር ምልክትነት ያስቀመጠው፣ በዚያ ቦሃን በተባለ ሰው ስም የተሰየመ ትልቅ ድንጋይ ሊሆን ይችላል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:7

ዳቤር… የአኮር ሸለቆ… የአዱሚም ኮረብታ… ዓይንሳሚስ… ዓይንሮጌል… የቤን ሄኖም ሸለቆ… የራፋይም ሸለቆ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:9

ኔፍቶ… የዔፍሮን ተራራ… በኣላ… ቂርያት ይዓሪም… ሴይር ተራራ… ይዓሪም ተራራ… ክሳሎን… ቤት ሳሚስ… ተምና

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:11

አቃሮን… በኣላ ተራራ… የብኒኤል

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:13

ቂርያት አባቅ… ዳቤር… ቂርያት ሤፍር

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

አርባቅ…ዔናቅ… ሴሲን… አኪመን… ተላሚን

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የኤናቅ ሶስት ወንድ ልጆች፡ ሴሲን፣ አኪመን እና ተላሚን ናቸው፤ እነዚህ የአናቅ ትውልድ ናቸው

እነዚህ ስሞች የሴሲን፣ አኪመን እና ተላሚን ጎሳ የነበሩ ትውልዶችን ይወክላሉ፡፡ በዚህ ዐውድ "ልጆች" እና "ትውልዶች" የሚሉት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም ይሰጣሉ፡፡ "የኤናቅ ትውልድ የሆኑት ሶስቱ ጎሳዎች፣ ሴሲን፣ አኪመን እና ተላሚን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ከዚያ ተነስቶ ወጣባቸው

"ከዚያ ተነስቶ ሊወጋቸው ወጣ"

Joshua 15:16

ቂርያትሤፍር

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ዓክሳ

ይህ የሴት ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ጎቶንያል… ቄኔዝ

እነዚህ የወንድ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:18

ዓክሳ ወደ ጎቶንያል መጣች

ይህ ዓክሳ የጎቶንያ ሚስት እንደምትሆን የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡ "ዓክሳ የጎቶንያ ሚስት በሆነች ጊዜ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አባቷ የእርሻ መሬት እንዲሰጠው ይጠይቅ ዘንድ ገፋፋችው

ይህ ቀጥተኛ ንግግር ሆኖ ሊተረጎም ይችላል፡፡ " ‘የእርሻ መሬት እንዲሰጠኝ አባቴን ለምነው' በማለት ገፋፋችው" (ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆኑ ትምህርተ ጥቅሶች

Joshua 15:19

የላይኛውን ምንጮች እና የታችኛውን ምንጮች

"የላይኛው" እና "የታችኛው" የሚሉት ቃላት በአመዛኙ የውሃ ምንጮቹን መልከዓ ምድራዊ ከፍታ የሚያመለክቱ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡

Joshua 15:20

ይህ የይሁዳ ነገድ ርስት ነበር

የይሁዳ ነገድ የተቀበለው ርስት የተገለጸው ቋሚ ሃብታቸው አድርገው እንደተቀበሉት ርስት ተደርጎ ነው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:21

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሰውን ደቡባዊ ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ ይህ ዝርዝር እስከ ኢያሱ 15፡32 ድረስ ይቀጥላል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:25

አያያዥ ሃሳብ፡

የከተሞቹ ስም ዝርዝር ይቀጥላል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:29

አያያዥ ሃሳብ፡

የከተሞቹ ስም ዝርዝር ይቀጥላል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:33

አጠቃላይ መረጃ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሰውን ሰሜናዊ ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:37

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:40

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:42

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:45

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሰፈራዎች

መንደሮች

የግብጽ ጅረት

በግብጽ አጠገብ፣ በምድሪቱ ደቡባዊ ምዕራብ ዳርቻ የሚገኝ ትንሽ የወንዝ ውሃ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:48

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:52

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:55

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:58

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:60

አያያዥ ሃሳብ፡

ጸሐፊው ይሁዳ የወረሳቸውን ከተሞች ይዘረዝራል፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 15:63

እስከ ዛሬ

ይህ የሚያመለክተው ጸሐፊው ይህንን መጽሐፍ እስከ ጻፈበት ጊዜ ድረስ ያለውን ወቅት ነው


Chapter 16

1 የዮሴፍም ልጆች የመሬት ድልድል በኢያሪኮ አጠገብ በምሥራቁ በኩል ካለው ከዮርዳኖስ አንሥቶ በምድረ በዳውና በተራራማው በኩል ከኢያሪኮ ወደ ቤቴል ወጣ። 2 ከቤቴል ወደ ሎዛ ወጣ፥ በአርካውያንም ዳርቻ በኩል ወደ አጣሮት አለፈ። 3 ወደ ምዕራብም እስከ የፍርሌጣውያን ዳርቻ እስከ ታችኛው ቤት ሖሮን ዳርቻ እስከ ጌዝር ድረስ ዘልቆ፥ መጨራሻውም በባሕሩ አጠገብ ነበር። 4 የዮሴፍም ነገድ ምናሴና ኤፍሬም ርስታቸውን የተቀበሉት በዚህ መንገድ ነበር። 5 የኤፍሬምም ነገድ ድንበር በየወገኖቻቸው እንደዚህ ነበረ፦ በምሥራቅ በኩል የርስታቸው ድንበር አጣሮት አዳር እስከ ላይኛው ቤት ሖሮን ድረስ ነበረ፤ 6 ከዚያ ወደ ባሕሩ ቀጠለ። ድንበሩም ወደ ምዕራብ ወደ ሚክምታት በሰሜን በኩል ወደ ምሥራቅ ወደ ተአናት ሴሎ ዞረ፥ ከዚያም ወደ ኢያኖክ በምሥራቅ በኩል አለፈ። 7 ከኢያኖክም ወደ አጣሮትና ወደ ነዓራት ወረደ፤ ወደ ኢያሪኮም ደረሰ፥ ወደ ዮርዳኖስም ወጣ። 8 ድንበሩም ካታጱዋ ወደ ምዕራብ እስከ ቃና ወንዝ ድረስ አለፈ፥ መውጫውም በባሕሩ መጨራሻ ነበረ። የኤፍሬም ነገድ ርስት በየወገኖቻቸው ይህ ነበረ፤ 9 ይኸውም፥ በምናሴ ነገድ ርስት መካከል ለኤፍሬምም ልጆች ከተለዩ ከተሞች ጋር፥ ከተሞች ሁሉ ከመንደሮቻቸው ጋር ነው። 10 በጌዝርም የተቀመጡትን ከነዓናውያንን አላሳደዱአቸውም ነበር፤እስከ ዛሬም ድረስ ከነዓናውያን በኤፍሬም መካከል ተቀምጠዋል፤ሆኖም እነዚህ ሰዎች የጉልበት ሥራ እንዲሠሩ ተደርገው ነበር።



Joshua 16:1

የዮሴፍ ነገድ

"የዮሴፍ ነገድ" በውስጡ፣ የዮሴፍን ሁለት ልጆች ነገዶች ማለት የምናሴ እና ኤፍሬም ነገዶችን ይይዛል፡፡ የምናሴ ነገድ እኩሌታ አስቀድሞ በዮርዳኖስ ምስራቅ የሰፈረ በመሆኑ፣ ይህ ሀረግ የሚያመለክተው የኤፍሬምን ነገድ እና የምናሴን ነገድ እኩሌታ ነው፡፡ "የኤፍሬም ነገድ እና የቀረው ሌላው ግማሽ የምናሴ ነገድ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ሎዛ… አጣሮት

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

አርካውያን

ይህ የአንድ ቡድን ሰዎች የወል ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 16:3

ፍሌጣውያን

ይህ የአንድ ቡድን ሰዎች የወል ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ታችኛው ቤትሓሮን… ጌዝር

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የዮሴፍ ነገዶች፣ ምናሴ እና ኤፍሬም

"የዮሴፍ ልጆች፣ የምናሴ እና ኤፍሬም ነገዶች"

ርስታቸውን ተቀበሉ

የምናሴ እና ኤፍሬም ነገዶች የያዙት ምድር የተገለጸው እንደ ቋሚ ሀብታቸው አድርገው እንደተቀበሉት ተደርጎ ነው፡፡ "ይህንን ምድር ርስታቸው አድርገው ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 16:5

በየ ጎሳው የኤፍሬም ነገድ ድንበር

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ለጎሳቸው የሰጠው ድንበር" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

አጣሮት አዳር…የላይኛው ቤት ሖሮን… ሚክምታት…ተአናት ሴሎ …ኢያኖክ…ነዓራት

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 16:8

ታጱዋ… ቃና

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ የኤፍሬም ነገድ ርስት ነበር

ኤፍሬም የያዘው ምድር የተገለጸው ቋሚ ሀብታቸው አድርገው እንደተቀበሉት ተደርጎ ነበር፡፡ "የኤፍሬም ነገድ ርስቱ አድርጎ የተቀበለው ምድር ይህ ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በየጎሳው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ለጎሳቸው የሰጠው" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

የተመረጡ ከተሞች

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ የመረጣቸው ከተሞች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ )

በምናሴ ጎሳ ውርስ ውስጥ

የምናሴ ነገድ የያዙት ምድር የተገለጸው እንደ ቋሚ ሀብታቸው አድርገው እንደተቀበሉት ተደርጎ ነው፡፡ "የምናሴ ነገድ ርስቱ አድርጎ በተቀበለው ምድር ውስጥ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 16:10

እስከ ዛሬ ድረስ

ይህ የሚያመለክተው ጸሐፊው ይህንን መጽሐፍ እስከ ጻፈበት ጊዜ ድረስ ያለውን ወቅት ነው

ይህ ህዝብ የጉልበት ስራ እንዲሰራ ይገደድ ነበር

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "እስራኤላውያን እነዚህን ሰዎች ባሪያ ሆነው እንዲያገለግሉ ያስገድዷቸው ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ )


Chapter 17

1 ለምናሴ ነገድ የተመደበው ይህ ነበር፤ እርሱም የዮሴፍ በኩር ነበር። የምናሴም በኩር የገለዓድ አባት ማኪር ራሱም የገለዓድ አባት ነበር። የማኪርም ወገኖች የገለዓድና የባሳን ምድር ተሰጣቸው ምክንያቱም ማኪር የጦር ሰው ነበርና። 2 ለቀሩት ለምናሴ ልጆች በየወገኖቻቸው ለአቢዔዝር ልጆች፥ለኬሴግ ልጆች ለአሥሪኤል ልጆች፥ ለሴኬም ልጆች፥ ለአፌር ልጆች፥ልሸሚዳ ልጆች ተሰጣቸው። የዮሴፍ ልጅ የምናሴ ወንዶች ልጆች በየወገኖቻቸው የተሰጣቸው እነዚህ ናቸው። 3 ለምናሴ ልጅ፥ ለማኪር ልጅ፥ ለገለዓድ ልጅ፤ ለኦፌር ልጅ፥ ለሰለጰዓድግን ሴቶች ልጆች እንጂ ወንዶች ልጆች አልነበሩአቸውም የሴቶች ልጆቹም ስም ማህለህ፥ ኑዓ፥ ዔግላ፥ ሚልካ፥ ቲርጻ ነበረ። 4 እነርሱም ወደ ካህኑ ወደ አልዓዛር፥ ወደ ነዌ ልጅ ወደ ኢያሱና ወደ አለቆች ቀርበው እንዲህ አሉ፦ እግዚአብሔርም ሙሴን ከወንድሞቻችን ጋር ርስት እንዲሰጠን አዝዞ ነበር። ስለዚህ ትእዛዙን በመከተል በአባታቸው ወንድሞች መካከል ለእነዚያ ሴቶች ርስት ሰጣቸው። 5 በዮርዳኖስ ማዶ ካለው በገለዓድና በባሳን ምድር ለምናሴ አሥር የመሬት መደቦች ተመድቦ ነበር፤ 6 ምክንያቱም የምናሴ ሴቶች ልጆች ከወንዶቹ ጋር ርስት ተቀብለዋል። የገለዓድም ምድር ለቀሩት ለምናሴ ነገድ ተመደበ። 7 የምናሴም የድንበር ክልል ከአሴር ጀምሮ በሴኬም ፊት ለፊት እስካለው እስከ ሚክምታት ድረስ ደረሰ። ድንበሩም በምዕራብ በኩል ወደ ታጱዋ ምንጭ አጠገብ ወደሚኖሩ ሰዎች አለፈ። 8 (የታጱዋ ምድር ለምናሴ ነበረ፤ በምናሴ ዳርቻ ያለው ታጱዋ ከተማ ግን ለኤፍሬም ነገድ ሆነ።) 9 ድንበሩም ወደ ቃና በኩል ወደ ታች ወረደ። እነዚህ ከወንዙ በስተደቡብ ያሉ ከተሞች በምናሴም ከተሞች መካከል ለኤፍሬም ሆኑ። የምናሴም ድንበር በወንዙ በስተሰሜን በኩል ሆኖ በባሕሩ መጨራሻ ነበረ። 10 በደቡብ በኩል ያለው ለኤፍሬም ነበረ፥ በሰሜንም በኩል ያለው ለምናሴ የነበረው ድንበሩ ባሕር ነበረ። በሰሜን በኩል ወደ አሴር፥ በምሥራቅ ም በኩል ወደ ይሳኮር ደረሰ። 11 በይሳኮርና በአሴር መካከል ቤት ሳንና መንደሮችዋን፥ ይብልዓምንና መንደሮችዋን፥ ዶር ሰዎችንና መንደሮችዋን ፥ የዓይንዶር ሰዎችንና መንደሮችዋን፥ የታዕናክ ሰዎችንና መንደሮችዋን ፥ የመጊዶ ሰዎችንና መደሮችዋን ፥ ሦስቱ ኮረብቶች ምናሴ ወረሳቸው። 12 ሆኖም የምናሴ ነገድ ግን እነዚህን ከተሞች ርስት አድርጎ ሊወስዳቸው አልቻሉም፤ ምክንያቱም ከነዓናውያን በዚያ ምድር መኖራቸውን ቀጥለው ነበር። 13 የእስራኤልም ሕዝብ እየጠነከሩ በመጡ ጊዜ ከነዓናውያንን የጉልበት ሥራ እንዲሠሩ አደረጉአቸው፤ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ከምካከላቸው እንዲወጡ አላደረጉም ነበር። 14 ከዚያም የዮሴፍ ልጆች ኢያሱን እንዲህ ብለው ተናገሩ፦ እኛ ብዙ ሕዝብ ሆነን ሳለን፥ እግዚአብሔርም ባርኮን እያለ ለምን አንድ ክፍል፥ አንድም ዕጣ ብቻ ርስት አድርገህ ሰጠኸን? አሉት። 15 ኢያሱም እንዲህ አላቸው፦ በቁጥር ብዙ ሕዝብ ከሆናችሁ፥ ወደ ዱር ወጥታችሁ በፌርዛውያንና በራፋይም ምድር ለራሳችሁ መንጥሩ። ተራራማውም የኤፍሬም አገር ጠብቦአችሁ እንደ ሆነ ይህንን አድርጉ። 16 የዮሴፍም ልጆች እንዲህ አሉ፦ '"ተራራማውም አገር አይበቃንም። ነገር ግን በሸለቆውም ውስጥ ለሚኖሩት፥ በቤት ሳንና በመንደሮችዋ በኢይዝራኤልም ሸለቆ ለሚኖሩት ከነዓናውያን የብረት ሰርገሎች አላቸው።" 17 ከዚያም ኢያሱ ለዮሴፍ ልጆች መለሰላቸው፦ ለመሆኑ ለኤፍሬምና ለምናሴ እናንተ ብዙ ሕዝብ ናችሁ፥ ጽኑም ኃይልም አላችሁ። አንድ ክፍል መሬት ብቻ ሊኖራችሁ አይገባም። 18 ተራራማውም አገር ለእናንተ ይሆናል። ዱር እንኳ ቢሆንም ትመነጥሩአቸዋላችሁ፥ ለእናንተም እንዲሆኑ ታደርጋላችሁ። ከነዓናውያንም የብረት ሰረገሎች ያሉአቸውና ኃይለኞች ቢሆኑም ልታስለቅቁአቸው ትችላላችሁ። ታሳድዳቸዋላችሁ አላቸው።



Joshua 17:1

በኩር እና እርሱ ራሱ ነበር

እዚህ ስፍራ "ራሱ" የሚለው የሚያጎላው ይንኑ ሰው ነው - ማኪር የምናሴ በኩር ነበር፣ እርሱ ራሱ የገለዓድም አባት ነበር፡፡ "እርሱ በኩርም ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ደጋጋሚ/ሪፍሌክቲቭ ተውላጠ ስም የሚለውን ይመልከቱ)

ማኪር…አቢዔዝር፣ ኬሌግ፣ አሥሪኤል፣ ሴኬም፣ ኦፌር እና ሸሚዳ

እነዚህ የወንድ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ለማኪር ትውልዶች የገለዓድ እና ባሳን ምድር ተሰጣቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ የገለዓድን እና የባሳን ምድር ለማኪር ተውልዶች ሰጣቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ )

ምድሪቱ ተሰጠች… ለጎሳቸው ተሰጠች

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ምድሪቱን አወረሰ… እናም ለጎሳቸው ሰጠ" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ )

Joshua 17:3

ሰለጰኣድ… ኦፌር… አልኣዛር

እነዚህ የወንድ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ማህለህ፣ ኑዓ፣ ዔግላ፣ ሚልካ፣ እና ቲርጻ

እነዚህ የሴት ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእኛ ርስት ለመስጠት

ምድሪቱ የተገለጸችው ሰዎቹ በቋሚነት እንደሚወርሷት ተደርጎ ነው፡፡ "ለእኛ ጥቂት መሬት ርስት አድርጎ ለመስጠት" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ለእነዚያ ሴቶች ርስት ሰጣቸው

ሊሰጡ የሚችሉ ትርጉሞች 1) "ኢያሱ ለእነዚያ ሴቶች ርስት ሰጣቸው" ወይም 2) "አልዓዛር ለእነዚያ ሴቶች ርስት ሰጣቸው" የሚሉ ናቸው፡፡

Joshua 17:5

አስር ቁራሽ መሬት ተሰጠ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ አስር ቁራሽ መሬት ሰጠ" (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ )

አስር ቁራሽ

"አስር ክፍሎች/ድርሻ"

ርስት ተቀበሉ

ምድሪቱ የተገለጸችው እንደ ቋሚ ሀብት እንደተቀበሏት ተደርጎ ነው፡፡ "ምድሪቱን ርስት አድርገው ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የገለዓደ ምድር ተሰጠች

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ የገለዓድን ምድር ሰጠ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 17:7

በስተ ደቡብ

በስተ ደቡብ በኩል

ሚክምታት… ታጱዋ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 17:9

ድንበሩ

"የምናሴ ምድር ድንበር"

ጅረት

በጣም ትንሽ ወንዝ

ቃና

የጅረት ስም (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በስተ ሰሜን አሴር ሊደረስ ይችላል

ሊሰጡ የሚችሉ ትርጉሞች 1) በስተ ሰሜን የምናሴ ምድር ዳርቻ እስከ አሴር ነገድ ምድር ሊደርስ ይችላል ወይም 2) አሴር ለመድረስ ወደ ሰሜን መጓዝ ይኖርበታል፡፡ "አሴር በስተ ሰሜን ይገኛል" ወይም "አሴር ለመድረስ ወደ ሰሜን መጓዝ ያስፈልጋል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ ምስራቅ፣ ይሳኮር

ግሱ በፊተኛው ሀረግ ይገኛል፡፡ "በስተ ምስራቅ፣ ወደ ይሳኮር ሊደረስ ይቻላል" (የተዘለለ/የተተወ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 17:11

ቤትሳን… ይብልዓም… ዶር… ታዕናክ… መጊዶ… ናፎት

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 17:14

የዮሴፍ ትውልዶች

ይህ የኤፍሬም እና ምናሴን ነገዶች ያመለክታል፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ያህዌ ባርኮን ሳለ…ለምን አንድ ብቻ ሰጠኸን?

የኤፍሬም እና የምናሴ ነገድ ሰዎች ይህንን ጥያቄ የጠየቁት ኢያሱ ለእነርሱ ተጨማሪ መሬት መስጠት እንደሚገባው አጽንኦት ለመስጠት ነው፡፡ "ያህዌ ባርኮናልና…ከአንድ በላይ ልትሰጠን ይገባ ነበር፡፡" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

አንድ እጅ መሬትና ርስት የሚሆን ድርሻ/አንድ ክፍል

እነዚህ ሁለት ሀረጎች በመሰረቱ ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፡፡ በሁለተኛው ሀረግ፣ ምድሩ የተገለጸው ህዝቡ ቋሚ ሀብት አድርጎ እንደተቀበለው ነው፡፡ " አንድ እጅ መሬት የእኛ ርስት ተደርጎ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ጥንድ ትርጉም እና ዘይቤያዊ አነጋጋር የሚሉትን ይመልከቱ)

ድርሻ

ክፍል

ህዝቡ በቁጥር ብዙ

"ብዙ ህዝብ"

እናንተ በቁጥር ብዙ ህዝብ ከሆናችሁ

"በቁጥር ብዙ ህዝብ እስከ ሆናችሁ ድረስ"

ራፋይም

የአንድ ቡድን ሰዎች የወል ስም፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 17:16

ቤት ሳን… ኢይዝራኤል

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የዮሴፍ ቤት

እዚህ ስፍራ "ቤት" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ትውልዶችን ነው፡፡ "የዮሴፍ ትውልዶች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት)

ትመነጥሩታላችሁ

"የዱሩን ዛፎች ትመነጥራላችሁ" ወይም "ዛፎቹን ትቆርጣላችሁ/ትመነጥራላችሁ"


Chapter 18

1 የእስራኤል ልጆች ማኅበር ሁሉ በሴሎ ተሰበሰቡ። በዚያም የመገናኛውን ድንኳን ተከሉ፤ ምድሩም ጸጥ ብሎ ተገዛላቸው። 2 ከእስራኤልም ልጆች መካከል ያልተካፈሉ ሰባት ነገዶች ቀርተው ነበር። 3 ኢያሱም ለእስራኤል ሰዎች አላቸው፦ የአባቶቻቸሁ እግዚአብሔር አምላክ የሰጣችሁን ምድር ትወርሱ ዘንድ እስከ መቼ ድረስ ቸል ትላላችሁ? 4 ከየነገዱም ሦስት ሦስት ሰዎች ምረጡ፥ እኔም እልካቸዋለሁ። ተነሥተውም የምድሪቱን ላይና ታች ይለካሉ። እንደ ርስታቸውም መጠን ይጽፉታል፤ ወደ እኔም ይመለሳሉ። 5 በሰባትም ክፍል ይከፍሉታል። ይሁዳም በደቡብ ድንበር ባሉበት ይጸናሉ፤ የዮሴፍ ወገኖች በሰሜን በኩል በዳርቻው ውስጥ ይቀጥላሉ። 6 እናንተም ምድሪቱን በሰባት ክፍል ትጽፋላችሁ፥ የጻፋችሁትንም ወደ እኔ ታመጣላችሁ፤ በአምላካችንም በእግዚአብሔር ፊት ዕጣ አጣጥላችኋለሁ። 7 ለሌዋውያንም ርስት የላቸውም፤ የእግዚአብሔር ክህነት ርስታቸው ነውና። የጋድም፥ የሮቤልም፥ የምናሴም ነገድ እኩሌታ ከዮርዳኖስ ማዶ ተቀበሉ።ይህም የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ የሰጣቸው ርስታቸው ይህ ነው። 8 ሰዎችም ተነሥተው ሄዱ፤ ኢያሱም ምድሩን ሊጽፉ የሄዱትን እንዲህ ብሎ አዘዛቸው፦ ሂዱ፥ በምድሩም ላይና ታች ዞራችሁ ጻፉት፥ ከዚያም ወደ እኔ ተመለሱ። በዚህም በሴሎ በእግዚአብሔር ፊት ዕጣ አጣጥላችኋለሁ። 9 ሰዎቹም ሄደው ምድሩን ላይና ታች ዞሩ። እንደ ከተሞችም በሰባት ክፍል ከፈሉት፥ ዝርዝራቸውንም ጻፉት። ከዚያም ኢያሱ ወደ ሰፈረበት ወደ ሴሎ ተመለሱ። 10 ኢያሱም በእግዚአብሔር ፊት በሴሎ ዕጣ አጣጠላቸው። በዚያም ኢያሱ ለእስራኤል ልጆች እንደ ክፍሎቻቸው ምድሩን አካፈላቸው። 11 የምድሩም ዕጣ ለብንያምም ነገድ በየወገኖቻቸው ተሰጠ። የዕጣቸውም ዳርቻ በይሁዳ ልጆችና በዮሴፍ ልጆች መካከል ነበረ። 12 በሰሜን በኩል ድንብራቸው ከዮርዳኖስ ይጀራል። ድንበሩም ወደ ኢያሪኮ ወደ ሰሜን በኩል፥በተራራማው አገር ወደ ምዕራብ ደረሰ። መውጫውም በቤት አዌን ምድረ በዳ ነብረ። 13 ድንበሩም ከዚያ በደቡብ በኩል ቤቴል ወደምትባል ወደ ሎዛ አለፈ። ድንበሩም በታችኛው ቤት ሖሮን በደቡብ በኩል ባለው ተራራ ወደ አጣሮት አዳር ወረደ። 14 ድንበሩም ወደ ምዕራብ ዘለቀ፥ በቤⶆሮንም ፊት ለፊት ካለው ተራራ ወደ ደቡብ ይዞራል፤ መውጫውም ቂርታትይዓሪም በትባል በይሁዳ ልጆች ከተማ በቂርያት በኣል ነበረ፤ ይህ የምዕራቡ ዳርቻ ነበረ። 15 የደቡብም ዳርቻ ከቂርያት ይዓሪም ውጪ ይጀምራል። ድንበሩም በምዕራብ በኩል ወደ ነፍቶ ውኃ ምንጭ ሄደ። 16 ድንበሩም በበን ሄኖም ሸለቆ ፊት ለፊት ወዳለው ተራራ መጨረሻ ወረደ፥ እርሱም በራፋይም ሸለቆ በሰንን በኩል ነው፤ ወደ ሄኖም ሸለቆ ወደ ኢያቡስ ዳር በደቡብ በኩል ወረደ፥ ወደ ዓይን ሮጌልም ወረደ። 17 ወደ ሰሜንም ዞረ፤ በኢን ሳሚስ አቅጣጫ በአዱሚም ዐቀበት ፊት ለፊት ወዳለው ወደ ጌሊሎትወጣ፤ ከዚያሜ ወደ ሮቤ ልጅ ወደ ቦሀን ድንጋይ ወረደ፤ 18 በሰሜንም ወገን ወደ ዓረባ አጠገብ አለፈ፥ ወደ ዓረባም ወረደ። 19 ድንበሩም ወደ ቤት ሖግላ ወደ ሰሜን በኩል አለፈ። መውጫውም በዮርዳንስ መጨረሻ በደቡብ በኩል ባለው በጨው ባሕር ልሳን አጠገብ ነበር፥ ይህም የደቡቡ ዳርቻ ነበረ። 20 በምሥራቅም በኩል ድንበሩ ዮርዳኖስ ነበረ። ይህ በዙሪያቸው ዳርቻ በየወገኖቻቸው የብንያም ልጆች ርስት ነበረ። 21 የብንያምም ልጆች ነገድ ከተሞች በየወገኖቻችቸው እነዚህ ነበሩ፦ ኢያሪኮ፥ ቤት ሖግላ፥ ዓመቀጺጽ፥ 22 ቤት ዓረባ፥ ዘማራይም፥ ቤቴል፥ 23 ዓዊም፥ ፋራ፥ ኤፍራታ፥ 24 ክፊርዓሞናይ፥ ዖፍኒ፣ ጋባ፤ አሥራ ሁለት ከተሞችና መንደሮቻቸው። 25 ገባዖን፥ ራማ፥ ብኤሮት፥ 26 ምጽጳ፥ ከፊራ፥አሞቂ፥ 27 ፍርቄም፥ይርጵኤል፥ ተርአላ፥ 28 ዼላ፥ ኤሌፍ፥ ኢየሩሳሌም የምትባልየኢያቡስ ከተማ፥ ቂርያትጊብዓት፤ አሥራ ሦስት ከትሞችና መንደሮቸችው። የብንያም ልጆች ርስት በየወገኖቻቸው ይህ ነበረ።



Joshua 18:1

እነርሱም ምድሪቱን ያዙ

የመገናኛ ድንኳኑን ከመትከላቸው አስቀድሞ በምድሪቱ የሚኖሩ ሰዎችን ማረኩ፡፡ "ምድሪቱን ከማረኩ በኋላ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (የትዕይንቶች ቅደም ተከተል የሚለውን ይመልከቱ)

ርስት ያልተሰጣቸው

ነገዶቹ የሚቀበሉት መሬት የተገለጸው በቋሚነት እንደተቀበሉት ሀብት ተደርጎ ነው፡፡ ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ርስት አድርጎ መሬት ላልሰጣቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 18:3

የሰጣችሁን… እስከ መቼ ቸል ትላላችሁ

ኢያሱ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው እስራኤላውያን ምድሪቱን ለመውረስ እንዲነሳሱ ለማበረታታት ነው፡፡ "የሰጣችሁን … ለረጅም ጊዜ፣ ቸል ብላችኋል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

የላይኛውን እና የታችኛውን ምድር

"ላይኛው እና ታችኛው" የሚሉት ቃላት በየአቅጣጫው የሚል ትርጉም አላቸው፡፡ይህንን በኢያሱ 18፡4 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡"በምድሪቱ በሁሉም አቅጣጫ" ወይም "በምድሪቱ በሙሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ይገባናል የሚሉትን የርስት ድርሻ ይጻፉ

ይህ ማለት እያንዳንዱ ነገድ የሚቀበለውን የርስት ድርሻ ይገልጻል ማለት ነው

ውርሳቸው

ሄደው የሚመለከቱት ምድር የተገለጸው እያንዳንዱ ነገድ እንደ ቋሚ ሀብት የሚወርሰው ተደርጎ ነው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:5

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ለእስራኤል ልጆች የሚያደርገውን ንግግር ቀጠለ

እነርሱ ይከፋከሉታል

"እነርሱ ምድሩን ይከፋፈላሉ"

ይሁዳ ይቀራል

"የይሁዳ ነገድ ይቀራል"

የዮሴፍ ቤት

እዚህ ስፍራ "ቤት" የሚለው ቃል የሚያመለክተው የዮሴፍን ትውልዶችን ነው፡፡ ይህ ሀረግ የኤፍሬምን እና ምናሴን ነገዶች ያመለክታል፡፡ "የኤፍሬም እና የምናሴ ትውልዶች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት እና ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 18:7

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ለእስራኤል ልጆች የሚያደርገውን ንግግር ቀጠለ

ምንም ድርሻ

"አንዳች የመሬት ድርሻ"

የያህዌ ካህን መሆናቸው የእነርሱ ርስት ነው

ኢያሱ ሌዋውያን ያህዌን በክህነት በማገልገል ያላቸውን ታላቅ ክብር ርስት አድርገው እንደሚወርሱት ነገር አድርጎ ይናገራል፡፡ "እነርሱ ያላቸው ድርሻ የያህዌ ካህን መሆን ነው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የምናሴ ግማሽ ነገድ

"የምናሴ ነገድ ግማሹ"

ርስታቸውን ተቀበሉ

ነገዱ የተቀበለው መሬት የተገለጸው ቋሚ ሀብታቸው አድርገው እንደተቀበሉት ነው፡፡ "ምድሪቱን ርስታቸው አድርገው ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡(ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:8

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ወደ ምድሪቱ ለሚሄዱ ለሃያ አንዱ ሰዎች ተናገረ

በምድሪቱ ላይ እና ታች

"ላይኛው እና ታችኛው" የሚሉት ቃላት በየአቅጣጫው የሚል ትርጉም አላቸው፡፡ይህንን በኢያሱ 18፡4 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡"በምድሪቱ በሁሉም አቅጣጫ" ወይም "በምድሪቱ በሙሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣው አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:10

ለእያንዳንዱ ድርሻው የሆነው ርስት ተሰጠው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ለእያንዳንዱ ነገድ ከምድሪቱ ድርሻ ድርሻውን ሰጠ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:11

በይሁዳ እና በየዮሴፍ ትውልዶች መሃል

"የይሁዳ ትውልዶች ርስት በሆነው ምድር እና የዮሴፍ ትውልዶች ርስት በሆነው ምድር መሃል"

የዮሴፍ ትውልዶች

ይህ የሚያመለክተው የኤፍሬምንና የምናሴን ትውልዶች ነው፡፡ (ይሆናል ተብሎ የሚገመት ዕውቀት እና በውስጠ ታዋቂነት የሚገኝ መረጃ የሚለውን ይመልከቱ)

ቤት አዌን

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:13

ድንበሩ… ዳርቻው

ይህ አንድ አይነት ነገርን ያመለክታል፡፡

ሎዛ… አጣሮት አዳር… ቤት ሖሮን… ቂርያት በኣል… ቂርያት ይዓሪም

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:15

ቂርያት ይዓሪም…ኤፍሮን…ነፍቶ…ቤን ሄኖን… ራፋይም… ሂኖም… ዓይን ሮጌል

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:17

ኢን ሳሚስ… ጌሊሎት…አዱ ሚም…ቤት ዐረባ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የቦሀን ድንጋይ

ይህ ምናልባት አንድ ሰው ለድንበር ምልክትነት ያስቀመጠው፣ በዚያ ቦሃን በተባለ ሰው ስም የተሰየመ ትልቅ ድንጋይ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህንን በኢያሱ 15፡6 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የቤት ዓረባ ትከሻ

የመሬቱ አቀማመጥ በስላች መልክ ወይም በጉብታ በመሆኑ ትከሻ እንደሆነ ተደርጎ ተገጽዋል፡፡ "የቤተ ዓረባ ስላች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:19

የቤት ሓግላን ሰሜናዊ ትከሻ

የመሬቱ አቀማመጥ በስላች መልክ ወይም በጉብታ በመሆኑ ትከሻ እንደሆነ ተደርጎ ተገጽዋል፡፡ "የቤተ ሓግላን ስላች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ቤትሖግላ

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ የብንያም ነገድ ርስት ነበር

የብንያም ነገድ የተቀበለው ምድር የተገለጸው ቋሚ ሀብታቸው አድርገው እንደተቀበሉት ተደርጎ ነው፡፡ "የብንያም ነገድ እንደ ርስት አድርጎ የተቀበለው ምድር ይህ ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ የተሰጠው በየጎሳው ነበር

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ለእያንዳንዱ ጎሳ ይህን ሰጠ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 18:25

አጠቃላይ መረጃ፡

ጸሐፊው በምድሪቱ የነበሩትን የብንያም ነገዶች ርስት አድርገው የተቀበሏቸውን ከተሞች መዘርዘሩን ቀጠለ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ የብንያም ርስት ነበር

የብንያም ነገድ የተቀበለው ምድር የተገለጸው ቋሚ ሀብታቸው አድርገው እንደተቀበሉት ተደርጎ ነው፡፡ "የብንያም ነገድ እንደ ርስት አድርጎ የተቀበለው ምድር ይህ ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 19

1 ሁለተኛውም ዕጣ ለስምዖን ልጆች ነገድ በየወገኖቻቸው ወጣ። ርስታቸውም በይሁዳ ልጆች ርስት መካከል ነበረ። 2 እነርዚህም ርስታቸው ሆኑላቸው፤ ቤርሳቤህም ሤባ፥ሞላዳ፥ 3 ሐጸርሹዕል፥ ባለ፥ዔጼም፥ 4 ኤልቶላድ፥ በቱል፥ ሔርማ፥ ጺቅላግ፥ 5 ቤትማርካቦት፥ ሐጸርሱሳ፥ 6 ቤተ ለባኦት፥ ሻሩሔን፤ አሥራ ሦስት ከተሞችና መንደሮቻቸው። 7 ዓይን፥ ሪሞን፥ ዔቴር፥ ዓሻን፤ አራት ከተሞችና መንደሮቻቸው፤ 8 እስከ ባዕላት ብኤርና እስከ ደቡቡ ራማት ድረስ በእነዚህ ከተሞችና ዙሪያ ያሉ መንደሮች ሁሉ። የስምዖን ልጆች ነገድ ርስት በየወገኖቻቸው ይህ ነበረ። 9 ከይሁዳ ልጆች ክፍል የስምዖን ልጆች ርስት ሆነ። የይሁዳም ልጆች ዕድል ፈንታ ስለ በዛባቸው የስምዖን ልጆች በርስታቸ መካከል ወረሱ። 10 ሦስተኛውም ዕጣ ለዛብሎን ልጆች በየወገኖቻቸው ወጣ። የርስታቸውም ድንበር ወደ ሣሪድ ደረሰ። 11 ድንበራቸውም በምዕራብ በኩል ወደ መርዓላ ወጣ፥ እስከ ደባሼትም ደረሰ፤ በዮቅንዓም ፊት ለፊት ወዳለው ወንዝ ደረሰ። 12 ከሣሪድም ወደ ፀሐይ መውጫ ወደ ምሥራቅ ወደ ኪስሎት ታቦር ዳርቻ ዞረ። ወደ ዳብራትም ወጣ፥ ወደ ያፊዓም ደረሰ። 13 ከዚያም በምሥራቅ በኩል ወደ ጋትሔፍርና ወደ ዒታቃጺን አለፈ፥ ወደ ሪምንና ወደ ኒዓ ወጣ። 14 ድንበሩም በሰሜን በኩል ወደ ሐናቶን ዞረ፥ መውጫውም በይፍታሕኤል ሸለቆ ነበረ። 15 ቀጣት፥ ነህላል፥ ሺምሮን፥ ይዳላ፥ ቤተ ልሔም፤ አሥራ ሁለት ከተሞችና መንደሮቻቸው። 16 የዛብሎን ልጆች ርስት በየወገኖቻቸው እነዚህ ከተሞችና መንደሮቻቸው ናቸው። 17 አራተኛውም ዕጣ ለይሳኮር ልጆች በየወገኖቻቸው ወጣ። 18 ድንበራቸውም ወደ ኢይዝራኤል፥ወደ ከስሎት፥ወደ ሱነም፥ 19 ወደ ሐፍራይም፥ ወደ ሺአን፥ ወደ አናሐራት፥ 20 ወደ ረቢት፥ ወደ ቂሶን፥ ወደ አቤጽ፥ 21 ሬሜት፥ ወደ ዓይንጋቢም፥ ወደ ዓይንሐዳ፥ ወደ ቤት ጳጼጽ ደረሰ፤ ድንበሩም ወደ ብቦርና ወደ ሻሕጽይማ፥ ወደ ቤት ሳሚስ ደረሰ። 22 የድንበራቸውም መውጫ ዮርዳኖስ ነበረ፤ አሥራ ስድስት ከተሞችና መንደሮቻቸው። 23 የይሳኮር ልጆች ነገድ ርስት በየወገኖቻቸው እነዚህ ከተሞችና መንደሮቻቸው ናቸው። 24 አምስተኛውም ዕጣ ለአሴር ልጆች ነገድ በየወገኖቻቸው ወጣ። 25 ድንበራቸውም ሔልቃት፥ ሐሊ፥ ቤጤን፥ አዚፍ፥ አላሜሌክ፥ ዓምዓድ፥ ሚሽአል ነበረ፤ 26 በምዕራብ በኩል ወደ ቀርሜሎስና ወደ ሺሖርሊብናት ደረሰ። 27 ወደ ፀሐይም መውጫ ወደ ቤት ዳጎን ዞረ፥ወደ ዛብሎንም ወደ ይፍታሕኤል ሸለቆ፥ በሰሜን በኩል ወደ ቤት ዓሜቅና ወደ ንዒኤልም ደረሰ፤ በስተ ግራ ቡልም ወደ ካቡል ወጣ። 28 ከዚያም ወደ ዔብሮን፥ ወደ ረአብ፥ ወደ ሐሞን፥ ወደ ቃና እስከ ታላቁ ሲኖናም ደረሰ። 29 ድንበርም ወደ ራማ፥ ወደ ተመሸገውም ከተማ ወደ ጢሮስ ዞረ፤ ድንበሩም ወደ ሖሳ ዞረ፤ መውጫውም በአክዚብ በኩል ወደ ባሕሩ ነበረ፤ 30 ዑማ፥ አፌቅ፥ ረአብ ደግሞ ነበሩ። እነዚህም ሀያ ሁለት ከተሞችና መንደሮቻቸው። 31 የአሴር ልጆች ነገድ ርስት በየወገኖቻቸው ከተሞችና መንደሮቻቸው ናቸው። 32 ስድስተኛውም ዕጣ ለንፍታሌም ልጆች በየወገኖቻቸው ወጣ። 33 ድንበራቸውም ከሔሌፍ፥ ከጸዕነኒም ዛፍ፥ ከአዳሚኔቄብ፥ ከየብኒኤል እስከ ለቁም ድረስ ነበረ፤ መውጫውም በዮርዳኖስ ነበረ። 34 ድንበሩም ወደ ምዕራብ ወደ አዝኖት ታቦር ዞረ፥ ከዚያም ወደ ሑቆቅ ወጣ፤ከዚያም በደቡም በኩል ወደ ዛብሎን፥ በምዕራብ በኩል ወደ አሴር፥ በዮርዳስም ወንዝ በፀሐይ መውጫ ወደ ይሁዳ ደረሰ። 35 የተመሸጉትም ከትሞች እነዚህ፦ ነበሩ ጺዲም፥ ጼር፥ ሐማት፥ ረቃት፥ ኬኔሬት፥ 36 አዳማ፥ ራማ፥ አሶር፥ 37 ቃዴስ፥ኤድራይ፥ ዓይንሐጽር፥ ይርአን፥ 38 ሚግዳልኤል፥ ሖሬም፥ ቤት ዓናት፥ ቤት ሳሚስ፤ አሥራ ዘጠኝ ከተሞችና መንደሮቻቸው ያልተቆጠሩ። 39 የንፍታሌም ልጆች ነገድ ርስት በየወገኖቻቸው እነዚህ ከተሞችና መንደሮቻቸው ናቸው። 40 ሰባተኛውም ዕጣ ለዳን ልጆች ነገድ በየወገኖቻቸው ወጣ። 41 የርስታቸውም ዳርቻ ይህ ነበረ፤ ጾርዓ፥ ኤሽታኦል፥ ዒርሼሜሽ፥ 42 ሸዕለቢን፥ ኤሎን፥ ይትላ፥ ኤሎን፥ 43 ተምና፥አቃሮን፥ 44 ኢልተቄ። ገባቶን።ባዕላት፥ ይሁድ፥ 45 ብኔንርቅ፥ ጋትሪሞ፥ 46 ሜያርቆን፥ በኢዮጴ ፊት ለፊት ካለው ዳርቻ ጋር ራቆን። 47 የዳንም ልጆች ዳርቻ አልበቃቸውም፥ የዳንም ልጆች ከሌሼም ጋር ሊዋጉ ወጡ፥ ያዙአትም፥ በሰይፍም ስለመቱአት፥ ወረሱአትም፥ ተቀመጡባትም። ስምዋንም በአባቶታቸው በዳን ስም ዳን ብለው ጠርአት። 48 የዳን ነገድ ርስት በየወገኖቻቸ እነዚህ ከትሞችና መንደሮቻቸው ናቸው። 49 ምድሩንም ሁሉ በየድንበሩ ርስት እንዲሆን ከፍለው ከጨረሱ በኋላ፥ የእስራኤል ልጆች ለነዌ ልጅ ለኢያሱ በመካከላቸው ርስት ሰጡት። 50 በኤፍሬም ተራራማ አገር ያለችውን ተምናሴራ የምትባለውን የፈለጋትን ከተማ እንደ እግዚአብሔር ትእዛዝ ሰጡት። ከተማውንም እንደ ገና ሠርቶ ተቀመጠበት። 51 ካህኑ አልዓዛር፥ የነዌም ልጅ ኢያሱ፥ የእስራኤልም ነገዶችና የአባቶች አለቆች በእግዚአብሔር ፊት በሴሎ በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ አጠገብ በዕጣ የተካፈሉት ርስት ይህ ነው። የምርሪቱንም ማከፋፈል ሥራ ጨረሱ።



Joshua 19:1

ሁለተኛው ዕጣ ሲጣል ለስምዖን ወጣ

"ኢያሱ ለሁለተኛ ጊዜ ዕጣ ሲጥል፣ ዕጣው የስምዖንን ነገድ አመለከተ"

ሁለተኛው

በዝርዝር ውስጥ ሁለተኛው ቁጥር (ተከታታይ ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

በየጎሳ በየጎሳው

"ኢያሱ ምድሪቱን ለእያንዳንዱ ጎሳ ሰጠ"

ውርሳቸው በይሁዳ ነገድ ርስት መሃል የሚገኝ ነበር፡፡

ምድሪቱ የተገለጸችው ነገዶቹ በቋሚነት የተቀበሏት ሃብት ተደርጋ ነው፡፡ "ርስት አድርገው የተቀበሉት ምድር የይሁዳ ነገድ ርስት አድርገው በተቀበሉት ምድር መሃል ነበር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:5

አጠቃላይ መረጃ፡

ጸሐፊው በምድሪቱ የነበሩትን የስምዖን ነገዶች ርስት አድርገው የተቀበሏቸውን ከተሞች መዘርዘሩን ቀጠለ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ጺቅላግ

የዚህችን ከተማ ስም በኢያሱ 15፡31 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ

Joshua 19:8

ይህ የስምዖን ነገድ ርስት ነበር

የስምዖን ነገድ የተቀበሏቸው ምድር እና ከተሞች የተገለጹት ቋሚ ርስታቸው አድርገው እንደ ተቀበሉት ሀብት ተደርጎ ነው፡፡ "የስምዖን ነገድ ርስታቸው አድርገው የተቀበሏቸው ምድር እና ከተሞች እነዚህ ነበሩ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በየጎሳ በየጎሳው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ለጎሳቸው የሰጣቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ለይሁዳ ነገድ ድርሻ ተደርጎ የተሰጠ ምድር

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ኢያሱ ለይሁዳ ነገድ ድርሻ አድርጎ የሰጠው ምድር " በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

የድርሻቸው መሃል

"የይሁዳ ምድር ድርሻ መሃል"

Joshua 19:10

ሦስተኛውን ዕጣ መጣል

ይህንን ሀረግ በኢያሱ 19፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ

ሦስተኛው

በዝርዝር ውስጥ ሦስተኛው ቁጥር (ተከታታይ ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ሣሪድ… መርዓላ… ደባሼት… ዮቅንዓም ከቅንዓም በተቃራኒ

"ቅንዓምን አቋርጦ"

Joshua 19:12

ሣሪድ…ኪስሎት ታቦር… ዳብራት… ያፊዓ… ጋት ሔፍር… ዒታ ቃጺን… ሪምን… ኒዓ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:17

አራተኛውን ዕጣ መጣል

ይህንን ሀረግ በኢያሱ 19፡1 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ

አራተኛው

በዝርዝር ውስጥ አራተኛው ቁጥር (ተከታታይ ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ከስሎት… ሱነም… ሐፍራይም… ሺኦን… አናሐራት

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:20

ረቢት… ቂሶን… አቤጽ…ሬማት…ዓይን ጋኒም… ዓይን ሐዳ… ቤት ጳጼጽ… ሻሕጹማ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ታቦር

ይህ የተራራ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:23

ይህ የይሳኮር ነገድ ርስት ነበር

የይሳኮር ነገድ የተቀበለው ምድር እና ከተማ የተገለጹት ቋሚ ርስት አድረገው እንደተቀበሏቸው ተደርጎ ነው፡፡ "ይህ የይሳኮር ነገድ ወርስ አድርጎ የተቀበለው ምድር እና ከተማዎች ናቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:24

አምስተኛውን ዕጣ መጣል

ይህንን ሀረግ በኢያሱ 19፡1 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ

አምስተኛው

በዝርዝር ውስጥ አምስተኛው ቁጥር (ተከታታይ ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ሔልቃት፣ ሐሊ፣ ቤጤን፣ አዚፍ፣ አላሜሌክ፣ ዓምዓድ፣ እና ሚሽአል… ሺሖር ሊብናት

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:27

ቤት ዳጎን…የይፍታሕ ኤል ሸለቆ… ቤት ዔሜቅ… ንዒኤል… ካቡል… አብዶን…ረአብ…ሐሞን…ቃና

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:29

ሖሳ… አክዚብ…ዑማ… አፌቅ…ረአብ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:31

ሖሳ… አክዚብ…ዑማ… አፌቅ…ረአብ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:32

ስድስተኛውን ዕጣ መጣል

ይህንን ሀረግ በኢያሱ 19፡1 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ

ስድስተኛው

በዝርዝር ውስጥ ስድስተኛው ቁጥር (ተከታታይ ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

ሔሌፍ…ጸዕነኒም…አዳሚ ኔቄብ… የብኒኤል…ለቄም…አዝኖት ታቦር…ሑቆቅ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:35

ጺዲም…ጼር… ሐማት… ረቃት… ኬኔሬት… አዳማ… ራማ… ሀዞር… ኤድራይ..ዓይንሐጾር

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሐማት

ይህ የሚገኘው በተመሳሳይ "ሐማት" ባለበት ሳይሆን፣ በገሊላ ባህር ምዕራብ የባህር ዳርቻ ነው፡፡

Joshua 19:38

ይርኦን… ሚግዳል ኤል… ሖሬም… ቤት ዓናት

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ የንፍታሌም ነገድ ርስት ነበር

የንፍታሌም ነገድ የተቀበለው ምድር እና ከተማ የተገለጹት ቋሚ ርስት አድረገው እንደተቀበሏቸው ተደርጎ ነው፡፡ "ይህ ንፍታሌም ነገድ ወርስ አድርጎ የተቀበለው ምድር እና ከተማዎች ናቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ሰባተኛውን ዕጣ መጣል

ይህንን ሀረግ በኢያሱ 19፡1 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ

ሰባተኛው

በዝርዝር ውስጥ ሰባተኛው ቁጥር (ተከታታይ ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የርስታቸው ግዛት/ክልል

የዳን ነገድ የተቀበለው ምድር የተገለጸው ቋሚ ርስት አድርገው እንደተቀበሉት ተደርጎ ነው፡፡ "የዳን ነገድ ወርስ አድርጎ የተቀበለው ርስት ግዛት/ክልል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)ጾርዓ፣ ኤሽታኦል፣ ዒር ሼሜሽ፣ ሸዕለቢን፣ ኤሎን፣ እና ይትላ እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:40

ሰባተኛውን ዕጣ መጣል

ይህንን ሀረግ በኢያሱ 19፡1 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ

ሰባተኛው

በዝርዝር ውስጥ ሰባተኛው ቁጥር (ተከታታይ ቁጥር የሚለውን ይመልከቱ)

የርስታቸው ግዛት/ክልል

የዳን ነገድ የተቀበለው ምድር የተገለጸው ቋሚ ርስት አድርገው እንደተቀበሉት ተደርጎ ነው፡፡ "የዳን ነገድ ወርስ አድርጎ የተቀበለው ርስት ግዛት/ክልል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)ጾርዓ፣ ኤሽታኦል፣ ዒር ሼሜሽ፣ ሸዕለቢን፣ ኤሎን፣ እና ይትላ እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:43

ኤሎን፣ ተምና፣ አቃሮን፣ ኢልተቄ፣ ገባቶን፣ ባዕላት፣ ይሁድ፣ ብኔ ብረቅ፣ ጋት ሪሞን፣ ሜያርቆን፣ እና ራቆን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ኢዮጴን ተሻግሮ

"ከኢዮጴ በተቃራኒ" ወይም "ከኢዮጴ አጠገብ

Joshua 19:47

ሌሼም

ይህ የከተማ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ይህ የዳን ነገድ ርስት ነበር

የዳን ነገድ የተቀበለው ምድር እና ከተማ የተገለጹት ቋሚ ርስት አድረገው እንደተቀበሏቸው ተደርጎ ነው፡፡ "ይህ የዳን ነገድ ወርስ አድርጎ የተቀበለው ምድር እና ከተማዎች ናቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:49

ለነዌ ልጅ ለኢያሱ በመሃላቸው ርስት ሰጡት

ኢያሱ የተቀበላት ከተማ የተገለጸችው ቋሚ ርስቱ አድርጎ እንደተቀበላት ርስቱ ተደርጎ ነው፡፡ "በምድራቸው ርስት አድርገው ለነዌ ልጅ ለኢያሱ ከተማ ሰጡት" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ተምና ሴራ

ይህ የከተማ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 19:51

የተሰጧቸው… ርስቶች እነዚህ ናቸው

የተለያዩ ነገዶች የተቀበሏቸው መሬት እና ከተሞች የተገለጹት ቋሚ ሀብት አድርገው እንደተቀበሏቸው ተደርጎ ነው፡፡ "ውርስ ተደርጎ የተሰጣቸው… ምድርና ከተሞች ድርሻቸው እነዚህ ናቸው፡፡" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 20

1 ከዚያም እግዚአብሔር ኢያሱን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 2 ለእስራኤልም ልጆች እንዲህ ብለህ ተናገራቸው፡ 3 ሳያውቅም ሰውን የገደለ እንዲሸሽባቸው በሙሴ እጅ የነገርኋችሁን የመማፀኛ ከተሞችን ለዩ። እነዚህም ከተሞች ከተገደለበት ከማንኛውም ከደም ተበቃይ የሚሸሹበት ቦታ ይሆኑላችኋል። 4 ከእነዚህም ከተሞች ወደ አንዲቱ ይሸሻል፥ በከተማይቱም በር አደባባይ ቆሞ ለከተማይቱ ሽማግሌዎች ጉዳዩን ያስረዳል። እነርሱም ወደ ከተማይቱ ይቀበሉታል፥ የሚኖርበትንም ስፍራ ይሰጡታል። 5 ሰው የሞተበትም ደም ተበቃዩ መጥቶ ለመበቀል ቢሞክር፥ የከተማውም ሰዎች ሰውየውን ለከተማው ባለሥልጣናት አሳልፈው መስጠት አይኖርባቸውም። ይህን ማድረግ የማይገባቸው እርሱ የገደለው ከዚህ በፊት ጥላቻ ሳይኖርና ሆነ ብሎ ባለመሆኑ ነው። 6 በማኅበሩ ፊት ለፍርድ እስኪቆም ድረስ፥ በዚያን ጊዜ ያለው በሊቀ ካህንነት የሚያገለግለው እስኪሞት ድረስ በዚያች ከተማ ይቀመጥ። ከዚያም ወዲያ ነፍሰ ገዳዩ ፥ ሸሽቶ ከነበረበት ከተማ ወደ ከተማውና ወደ ቤቱ ይመለሳል። 7 በንፍታሌም ባለው በተራራማው አገር በገሊላ ቃዴስን፥ በኤፍሬምም ባለው በተራራማው አገር ኬብሮን የምትባለውን ቂርያትአርባቅን ለዩ። 8 ከዮርዳኖስም ማዶ ከኢያሪኮ ወደ ምሥራቅ ከሮቤል ነገድ በምድረ በዳው በደልዳላው ስፍራ ቦሶርን፣ ከጋድም ነገድ በገለዓድ ራሞትን፥ ከምናሴም ነገድ በባሳን ቶላንን ለዩ። 9 ማንም ሰው ሳያውቅ ሰውን የገደለ ወደዚያ እንዲሸሽና በመካከላቸውም ለሚቀመጥ መጻተኛ ለእስራኤል ልጆች ሁሉ የተመረጡ ከተሞች እነዚህ ናቸው። ይህም ሰው በማኅብሩ ፊት ለፍርድ እስኪቆም ድረስ በደም ተበቃዩ እጅ እንዳይሞት ነው።



Joshua 20:1

በሙሴ እጅ

እዚህ ስፍራ "የሙሴ እጅ" የሚለው የሚያመለክተው ሙሴ የጻፋቸውን መጽሐፍት ነው፡፡ "ሙሴ በጻፋቸው ነገሮች አማካይነት" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ሳየስበው በድንገት የገደለ

x

Joshua 20:4

እርሱ ይሸሻል

እዚህ ስፍራ "እርሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሳያውቅ እንድን ሰው የገደለን ሰው ነው፡፡

ለከተማይቱ ሽማግሌዎች ጉዳዩን ያስረዳል

"ሰውየውን ሳያወቅ በድንገት እንደገደለው የከተማይቱን ሽማግሌዎች ያሳምናል/ያስረዳል"

ከዚይም እነርሱ እርሱን ይወስዱታል

"እነርሱ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሽማግሌዎችን ሲሆን "እርሱን" የሚለው የሚያመለክተው ሳያውቅ አንድን ሰው የገደለን ሰው ነው፡፡

በእነርሱ መሃል ይኖራል

ይህ ሽማግሌዎችን ብቻ ሳይሆን፣ ከተማይቱን በጭምር ያመለክታል፡፡

Joshua 20:5

የሟችን ደም መበቀል

እዚህ ስፍራ የአንድ ሰው የፈሰሰ ደም የሚለው የሚገልጸው መሞትን ነው፡፡ ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ ይህንን በኢያሱ 20፡3 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ "የሞተውን ሰው መበቀል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት እና አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚሉትን ይመልከቱ)

ወዳጁን/ጎረቤቱን ሳያውቅ የገደለ…በድንገት ሰውየውን የገደለ

እነዚህ ሀረጋት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው

በጉባኤው ፊት ይቁም

ይህ ሀረግ የሚገልጸው ፍትህን በመፈለግ አብረውት በሚኖሩ ወገኖቹ ችሎት ፊት መቆምን ነው

Joshua 20:7

አጠቃላይ መረጃ፡

በዚህ ክፍል ውስጥ በርካታ ስሞች አሉ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስም ነው

Joshua 20:9

በሌላ ሰው መገደል የለበትም

እዚህ ስፍራ "በእጅ" የሚለው ለአንድ ነገር ልዩ ምክንያት መሆን የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡ "መገደል የለበትም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የፈሰሰውን ደም መበቀል

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ ይህንን ሀረግ በኢያሱ 20፡3 እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ "የአንድን ሰው ሞት መበቀል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት እና አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚሉትን ይመልከቱ)


Chapter 21

1 ከዚያም የሌዋውያን ወገኖች አለቆች ወደ ካህኑ አልዓዘር፥ ወደ ነዌ ልጅ ኢያሱና ወደ እስራኤል ነገዶች አለቆች ቀርቡ። 2 እነርሱም በከነዓን ምድር ባለችው በሴሎ እንዲህ አሉአቸው፡- እግዚአብሔር በሙሴ እጅ የምንቀመጥባቸውንና ለከብቶቻችንም መሰማሪያ የሚሆኑ ከተሞች እንድትሰጡን አዞአችኋል። 3 ስለዚህም የእስራኤልም ሕዝብ በእግዚአብሔር ትእዛዝ የሚከተሉትን ከተሞች ለከብቶቻቸውም መሰማሪያ ጭምር እንዲሆኑ ርስታቸውን ለሌዋውያን ሰጡአቸው። 4 ለቀዓትም ወገኖች የዕጣው ውጤት እንዲህ ሆነ፦ ሌዋውያንም ለነበሩ ለካህኑ ለአሮን ልጆች፥ ከይሁዳ ነገድ ከስምዖንም ነገድ ከብንያምም ነገድ አሥራ ሦስት ከተሞች ተሰጣቸው። 5 ለቀሩትም ለቀዓት ልጆች ከኤፍሬም ነገድ፥ ከዳንም ነገድና ከምናሴ ነገድ እክኩሌታ አሥር ከተሞች በዕጣ ተቀበሉ። 6 ለጌድሶንም ልጆች ከይሳኮር ነገድ፥ ከአሴር ነገድ፥ ከንፍታሌምም ነገድ፥ በባሳን ካለው ከምናሴ ነገድ እኩሌታ አሥራ ሦስት ከተሞች በዕጣ ተሰጣቸው። 7 ለሜራሪም ልጅች በየወገኖቻቸው ከሮቤል ነገድ፥ከጋድ ነገድና ከዛብሎን ነገድአሥራ ሁለት ከተሞ ተቀበሉ። 8 እግዚአብሔርም በሙሴ እጅ እንዳዘዛቸው የእስራኤል ልጆች እነዚህን ከተሞችና መሰማሪያቸውን ለሌዋውያን በዕጣ ሰጡ። 9 ከይሁዳም ልጆች ነገድ ከስምዖንም ልጆች ነገድ በስማቸው እነዚህን ከተሞች ሰጡ። 10 እነዚህ ከተሞች ከሌዊ ልጆች ነገድ የቀዓት ወገን ለሆኑ ለአሮን ልጆች ተሰጥቶአቸው ነበር። የመጀመሪያው ዕጣ ለእነርሱ ወጥቶላቸው ነበር። 11 እንደ ኬብሮን ተመሳሳይ ቦታ በይሁዳ ተራራማ አገር ያለችውን ቂርያት አርባቅ (ይህም አርባቅ የዔናቅ አባት ነበረ) የምትባለውን ከተማ በዙሪያዋም ያለውን የከብቶች መሰማሪያዋን ሰጡአቸው። 12 የከተማይቱንም እርሻ ግን መንደሮችዋንም ለዮፎኒ ልጅ ለካሌብ ርስት አድርገው ሰጡት። 13 ለካህኑም ለአሮን ልጆች ሳያውቁ ነፍሰ ገዳይ ለሆኑት መማፀኛ ከተማ የሆነችውን ኬብሮንንና መሰማሪያዋን፥ ልብናን ከመሰማሪያዋን ጋር ሰጡ፤ 14 የቲርንና መሰማሪያዋን፥ ኤሽት ሞዓንና መሰማሪያዋን፥ 15 ሖሎንንና መሰማሪያዋን፥ ዳቤርንና መሰማሪያዋን፥ 16 ዓይንንና መሰማሪያዋን፥ ዮጣንና መሰማሪያዋን፥ ቤት ሳሚስንና መሰማሪያዋን ሰጡ። ከእነዚህ ከሁለቱ ነገዶች ዘጠኝ ከተሞችን ነበሩ። 17 ከብንያምም ነገድ ገባዖንንና መሰማሪያዋን፥ ናሲብንና መሰማሪያዋን፥ 18 ዓናቶትንና መሰማሪያዋን፥ አልሞንንና መሰማሪያዋን፤አራት ከተሞችን ሰጡ። 19 ለአሮን ልጆች ለካህናት የተሰጡ ከተሞች ከመሰማሪያቸው ባጠቃላይ አሥራ ሦስት ከተሞች ናቸው። 20 ለቀሩትም ለቀዓት ልጆች ወገኖች ሌዋውያን የተሰጣቸ ከተሞች ከኤፍሬም ነገድ ዕጣ ወጥቶላቸው ነበር። 21 ለእነርሱም በኤፍሬም ተራራማ አገር ሳያውቁ ነፍሰ ገዳይ ለሆኑት መማፀኛ ከተማ የሆነችውን ሴኬምንና መሰማሪያዋን፥ ጌዝርንና መሰማሪያዋን፥ 22 ቂብጻይምንና መስማሪያዋን፥ ቤት ሖሮንንና መሰማሪያዋን፤ አራቱን ከተሞች ሰጡአቸው። 23 ከዳንም ነገድ ኤልተቄንና መሰማሪያዋን፥ ገባቶንንና መሰማሪያዋን፥ 24 ኤሎንንና መሰማሪያዋን፥ ጋትሪሞንንና መሰማሪያዋን፤ አራቱን ከተሞች ሰጡአቸው። 25 ከምናሴም ነገድ እኩሌታ ታዕናክንና መሰማሪያዋን፥ ጋትሪሞንንና መሰማሪያዋን፤ ሁለቱን ከተሞች ሰጡአቸው። 26 ለቀሩት የቀዓት ልጆች ወገኖች የተሰጡ ከተሞች ሁሉ ከመሰማሪያቸውን ጋር አሥር ከተሞችናቸው። 27 ለሌሎች ሌዋውያንም ወገኖች ለጌድሶን ልጆች ከምናሴ ነገድ እኩሌታ ሳያውቁ ነፍሰ ገዳይ ለሆኑት መማፀኛ ከተማ በባሳን ውስጥ የሆነችውን ጎላንንና መሰማሪያዋን፥ በኤሽትራንና መሰማይያዋን ሁለቱን ከተሞች ሰጡአቸው። 28 ከይሳኮርም ነገድ ቂሶንንና መሰማሪያዋን፥ ዳብራትንና መሰማሪያዋን፥ 29 የያርሙትንና መሰማሪያዋን፥ ዓይንጋኒምንና መሰማሪያዋን፤ አራቱን ከተሞች ለጋሪሶን ነገድ ሰጡአቸው። 30 ከአሴርም ነገድ ሚሽአልንና መሰማሪያዋን፥ ዓብዶንና መሰማሪያዋን፥ 31 ሔልቃትንና መሰማሪያዋን፥ ረአብንና መሰማሪያዋን፤ አራቱን ከተሞች ሰጡአቸው። 32 ከንፍታሌምም ነገድ ሳያውቁ ነፍሰ ገዳይ ለሆኑት መማፀኛ ከተማ የሆነችውን በገሊላ ውስጥ ቃዴስንና መሰማሪያዋን፥ ሐሞትዶርንና መሰማሪያዋን፥ ቀርታንንና መሰማሪያዋን፤ ሦስቱን ከተሞች ለጌድሶን ነገድ ሰጡአቸው። 33 የጌድሶን ልጆች ከተሞች ሁሉ በየወገኖቻቸው ከመሰማሪያቸው ጋር አሥራ ሦስት ከተሞች ናቸው። 34 ከሌዋውያንም ለቀሩት ለሜራሪ ልጆች ወገን ከዛብሎን ነገድ ዮቅንዓምንና መሰማሪያዋን፥ ቀርታንና መሰማሪያዋን፥ 35 ዲሞናንና መሰማሪያዋን፥ ነህላልንና መሰማሪያዋን፤ አራቱን ከተሞች ሰጡ። 36 ለሜራሪ ነገድ ከሮቤልም ነገድ ቦሶርንና መሰማሪያዋን፥ ያሀጽንና መሰምሪያዋን፥ 37 ቅዴሞትንና መሰማሪያዋን፥ ሜፍዓትንና መሰማሪያዋን፤ አራቱን ከተሞች ሰጡ። 38 ሳያውቁ ነፍሰ ገዳይ ለሆኑት መማፀኛ ከተማ የሆነችውን ከጋድም ነገድ በገለዓድ ውስጥ ራሞትንና መሰማሪያዋን፥ መሃናይምንማ መሰማሪያዋን ሰጡ። 39 ሐሴቦንንና መሰማሪያዋን፥ ኢያዜርንና መሰማሪያዋን ሜራሪ ነገድ ደግሞ የተሰጡ ባጠቃላይ አራት ከተሞች ናቸው። 40 ከሌዋውያን ወገኖች የቀሩት የሜራሪ ልጆች ከተሞች ሁሉ በየወገኖቻቸው እነዚህ ነበሩ፤ ዕጣቸውም ባጠቃላይ አሥራ ሁለት ከተሞች ነበሩ። 41 በእስራኤል ልጆች ርስት መካከል የነበሩት የሌዋውያን ከተሞች ሁሉ አርባ ስምንት ከተሞችና መሰማሪያቸው ነበሩ። 42 እነዚህም ከተሞች እያንዳንዳቸው ከመሰማሪያቸው ጋር ነበሩ፤ እነዚህም ከተሞች ሁሉ በዚህ ዓይነት መንገድ ነበሩ። 43 እግዚአብሔርም ይሰጣቸው ዘንድ ለአባቶቻቸው የማለላቸውን ምድር ሁሉ ለእስራኤል ሰጠ። ወረሱአትም፥ ተቀመጡባትም። 44 እግዚአብሔርም ለአባቶቻቸው እንደ ማለላቸው በዙሪያቸው ካሉት አሳረፋቸው። ከጠላቶቻቸውም ሁሉ ይቋቋማቸው ዘንድ ማንም ሰው አልቻለም፤ እግዚአብሔርም ጠላቶቻቸውን ሁሉ በእጃቸው አሳልፎ ሰጣቸው። 45 እግዚአብሔር ለእስራኤል ቤት ከተናገረው መልካም ነገር ሁሉ ተፈጸመ እንጂ ምንም አልቀረም።



Joshua 21:1

አልዓዛር… ነዌ

እነዚህ ስሞች የወንድ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ለእነርሱ አሏቸው

"ሌዋውያን ለእነርሱ አሏቸው"

ያህዌ እናንተን በሙሴ እጅ አዘዛችሁ

"በእጅ" የሚለው ሀረግ ያህዌ ትዕዛዙን ለመስጠት/ማቅረብ ሙሴን እንደተጠቀመበት የሚገልጽ ፈሊጣ አነጋገር ነው፡፡ "ያህዌ ያዛችሁ ዘንድ ሙሴን ተናገረው/ አዘዘው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:3

ተከታዮቹ ከተሞች

ይህ የሚያመለክተው በተከታዮቹ ቁጥሮች የሚዘረዘሩትን/የሚጻፉትን ከተሞች ነው፡፡

Joshua 21:4

እጣ መጣል

ከመሪዎች ፍላጎት ውጭ በዕጣ ምርጫ የማድረግ ዘዴ ብዙውን ጊዜ የሚካሄደው እግዚአብሔር ውጤቱን ይወስን በሚል ሃሳብ ነው፡፡ ይህንን እንዴት በኢያሱ 19፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡

ቀዓታውያን

በዚህ ቡድን ውስጥ እነዚህ ካህናት የሌዊ ትውልድ የሆኑ የቀዓት ልጆች ነበሩ፡፡ ከእነርሱ ከፊሎቹም የአሮን ትውልድ፣ የቀዓት የልጅ ልጆች ነበሩ፡፡

አስራ ሶስት ከተሞች… አስር ከተሞች

የከተሞች ቁጥር (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ግማሽ ነገድ

የነገዱ ግማሽ የተባለበት ምክንያት ቀሪው ግማሽ ርስታቸውን ዮርዳኖስን ወንዝ ከማቋረጣቸው አስቀድሞ ስተቀበሉ ነው፡፡

Joshua 21:6

ጌርሶን

ጌርሶን ከሌዊ ልጆች አንዱ ነበር፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

እጣ መጣል

ከመሪዎች ፍላጎት ውጭ በዕጣ ምርጫ የማድረግ ዘዴ ብዙውን ጊዜ የሚካሄደው እግዚአብሔር ውጤቱን ይወስን በሚል ሃሳብ ነው፡፡ ይህንን እንዴት በኢያሱ 19፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡

ሜራሪ

ሜራሪ ከሌዊ ልጆች አንዱ ነበር፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:8

ያህዌ በሙሴ እጅ አዘዘ

"በእጅ" የሚለው ሀረግ ትርጉሙ ያህዌ ሙሴን ትዕዛዙን ለማቅረብ ተጠቀመበት ማለት ነው፡፡ "ያህዌ ሙሴ እንዲያዝ ነገረው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

የቀዓታውያን ነገዶች

በዚህ ቡድን ውስጥ እነዚህ ካህናት የሌዊ ትውልድ የሆኑ የቀዓት ልጆች ነበሩ፡፡ ከእነርሱ ከፊሎቹም የአሮን ትውልድ፣ የቀዓት የልጅ ልጆች ነበሩ፡፡ ይህንን እንዴት በኢያሱ 19፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡

Joshua 21:11

አርባቅ የኤናቅ አባት ነበር

ይህ መረጃ የቂርያት አርባቅን ከተማ ስለ መሰረታት ሰው ስም የቀረበ የመረጃ ዳራ ነው፡፡ (የመረጃ ዳራ የሚለውን ይመልከቱ)

ዔናቅ

ይህ የወንድ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ተራራማ አገር

ከተራሮች አነስ ያለ ተፈጥሯዊ ከፍታ ያለው ምድር

የግጦሽ መሬት/ የከብቶች መሰማሪያ

በሳር ወይም ለከብቶች ግጦሽ ተስማሚ በሆነ ተክል የተሸፈነ አካባቢ

የከተማይቱ መሰማሪያ

ብዙውን ጊዜ ተክሎች የሚገኙበት በከተማ ዙሪያ ሚገኝና የከተማይቱ ይዞታ የሆነ መሬት

መንደሮች

ብዙውን ጊዜ ከከተማ የሚያንስ፣ አነስተኛ ማህበረሰብ፡፡

Joshua 21:13

ልብናን… ቲርናን… ኤሽትሞዓን… ሖሎን… ዳቤር… ዓይን… ዮጣን

እነዚህ ሁሉ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ዘጠኝ ከተሞች… ሁለት ነገዶች

በክፍሉ/ምንባቡ ውስጥ የከተሞች እና የነገዶች ቁጥር

Joshua 21:17

ከብንያም ነገድ ገባዖን ተሰጠ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የብንያም ነገድ ገባዖንን ሰጠ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ገባዖን… አናቶት… አልሞን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

አስራ ሶስት ከተሞች

"13 ከተሞች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:20

የቀዓት ነገዶች

በዚህ ቡድን ውስጥ እነዚህ ካህናት የሌዊ ትውልድ የሆኑ የቀዓት ልጆች ነበሩ፡፡ ከእነርሱ ከፊሎቹም የአሮን ትውልድ፣ የቀዓት የልጅ ልጆች ነበሩ፡፡ ይህንን እንዴት በኢያሱ 19፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡

የተሰጧቸው ከተሞች ነበሯቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ከተሞችን ተቀበሉ/ተሰጧቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ዕጣ መጣል

ከመሪዎች ፍላጎት ውጭ በዕጣ ምርጫ የማድረግ ዘዴ ብዙውን ጊዜ የሚካሄደው እግዚአብሔር ውጤቱን ይወስን በሚል ሃሳብ ነው፡፡ ይህንን እንዴት በኢያሱ 19፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡

ጌዝር… ቂብጻይምን… ቤት ሖሮን

የከተሞች ስሞች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በጠቅላላው አራት ከተሞች

ይህ የሚያመለክተው የከተሞቹን ቁጥር ዝርዝር በአጠቃላይ ነው (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:23

ከዳን ነገድ፣ የቀዓት ነገድ ኤልተቄን ሰጧቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የዳን ነገድ ለቀዓት ኤልተቄን ሰጧቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

የቀዓት ነገድ

በዚህ ቡድን ውስጥ እነዚህ ካህናት የሌዊ ትውልድ የሆኑ የቀዓት ልጆች ነበሩ፡፡ ከእነርሱ ከፊሎቹም የአሮን ትውልድ፣ የቀዓት የልጅ ልጆች ነበሩ፡፡ ይህንን ተመሳሳይ ሀረግ በኢያሱ 21፡20 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ኤልተቄን… ገባቶን… ኤሎን….ጋት ሪሞን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

አራት ከተሞች

ይህ የከተሞቹን ቁጥር ያመለክታል፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:25

ከምናሴ ግማሽ ነገድ፣ የቀዓት ነገድ ታዕናክን ሰጧቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የምናሴ ነገድ እኩሌታ ለቀዓት ነገድ ታዕናክን ሰጧቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ታዕናክ… ጋት ሪሞን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሁለት ከተሞች… አስር ከተሞች

የተመዘገቡ ከተሞች ቁጥር (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

የቀዓት ነገድ…የቀዓታውያን ነገዶች

በዚህ ቡድን ውስጥ እነዚህ ካህናት የሌዊ ትውልድ የሆኑ የቀዓት ልጆች ነበሩ፡፡ ከእነርሱ ከፊሎቹም የአሮን ትውልድ፣ የቀዓት የልጅ ልጆች ነበሩ፡፡ ይህንን በኢያሱ 21፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:27

ከምናሴ ነገድ አንስቶ፣ እስከ ጌርሶን ጎሳ ድረስ እነዚህም ሌሎች የሌዊ ጎሳዎቸ ነበሩ እነርሱም ጎላንን ሰጡ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የምናሴ ነገድ እኩሌታ፣ ሌሎች የሌዊ ነገዶች ከምናሴ ነገድ እኩሌታ ጎላንን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ጎላን… በኤሽትራ

የከተሞች ስሞች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሌላውን ሳያውቅ የገደለ

ይህ የሚያመለክተው ሰውን ለመግደል ታስቦ ያልተደረገን ግድያ ነው

ሁለት ከተሞች

የከተሞች ቁጥር (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:28

ለጌርሶን ነገድም ቂሶን ሰጡ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የጌርሶን ነገድ ደግሞ ቂሶንን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ቂሶን… ዳብራት… የርሙት…ዓይን ጋኒም… ሚሽአል…ዓብዶን… ሔልቃት… ረአብ

የከተሞች ስሞች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ከአሴር ነገዶች፣ ሚሽአልን ሰጡ ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ከአሴር ነገድ ሚሽአልን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

በአጠቃላይ አራት ከተሞች

ይህ የሚያመለክተው የተመዘገቡ/የተዘረዘሩ ከተሞችን ዝርዝር ነው (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:32

ከንፍታሌም ነገድ ለጌርሶን ነገዶች ቃዴስን ሰጡ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የጌርሶን ከንፍታሌም ነገድ ቃዴስን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ጌርሶን

ይህ የሰው ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ሐሞት ዶር… ቀርታን

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በጠቅላላው አስራ ሶስት ከተሞች

"በጠቅላላው 13 ከተሞች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:34

ለተቀሩት ሌዋውያን- የሜራሪ ነገድ- ከዛብሎን ነገድ ድርሻ ዮቅናምን ሰጡ

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የተቀሩት ሌዋውያን- የሜራሪ ነገድ- ከዛብሎን ነገድ ዮቅናምን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ሜራሪ

ይህ የሰው ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ዮቅናም… ቀርታ…ዲሞና… ነህላል

የከተሞች ስሞች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በአጠቃላይ አራት ከተሞች

ከተሞቹ በጠቅላላው የተጠቀሱት እንደ ቁጥር ነው፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:36

ለሜራሪ ነገዶች ከሮቤል ነገዶች ቦሶር ተሰጣቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የሜራሪ ነገዶች ከሮቤል ነገዶች ቦሶርን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

አራት ከተሞች

ይህ የከተሞቹን ቁጥር ያመለክታል፡፡ (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ቦሶር…ያሀጽ… ቅዴሞት… ሜፍዓት…ራሞት

የከተሞች ስሞች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ከጋድ ነገድ ውስጥ ራሞት ተሰጣቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ከጋድ ነገድ ራሞትን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

መሃናይም

ይህ የከተማ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:39

የሜራሪ ነገዶችም ደግሞ ሐሴቦን ተሰጣቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "የሜራሪ ነገድ ደግሞ ሐሴቦንን ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ሐሴቦን…ኢያዜር

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በአጠቃላይ አስራ ሁለት ከተሞች

"በአጠቃላይ 12 ከተሞች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

በአጠቃላይ በዕጣ አስራ ሁለት ከተሞች ተሰጧቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "እነዚህን አስራ ሁለት ከተሞች በዕጣ መጣል ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

ዕጣ መጣል

ከመሪዎች ፍላጎት ውጭ በዕጣ ምርጫ የማድረግ ዘዴ ብዙውን ጊዜ የሚካሄደው እግዚአብሔር ውጤቱን ይወስን በሚል ሃሳብ ነው፡፡ ይህንን እንዴት በኢያሱ 19፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎሙት ይመልከቱ፡፡

Joshua 21:41

የሌዋውያን ከተሞች ከምድሪቱ መሃል የተሰጡ ናቸው

ይህ በአድራጊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ሌዋውያኑ ከተሞቻቸውን ከምድሪቱ መሃል ተቀበሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (አድራጊ ወይም ተደራጊ የሚለውን ይመልከቱ)

አርባ-ስምንት ከተሞች

"48 ከተሞች" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 21:43

ማለ

"መሃላ ሰጠ"

ከጠላቶቻቸው አንዳቸውም ሊያሸንፏቸው አይችሉም

ሃሳቡን ለማጉላት ይህ የተገለጸው በአሉታ ነው፡፡ "እነርሱ ጠላቶቻቸውን ሁሉ አሸነፉ" (ምፀት/ላይዶክስ የሚለውን ይመልከቱ)

ጠላቶቻቸውን ሁሉ በእጆቻቸው አሳልፎ ሰጣቸው

እዚህ ስፍራ "በእጆቻቸው" የሚለው "ከጉልበታቸው ስር አደረጋቸው/አንበረከከላቸው" ማለት ነው፡፡ "ጠላቶቻቸውን ሁሉ እንዲያሸንፉ ሃይል ሰጣቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት)

ያህዌ ለእስራኤል ቤት ቃል ከገባው መልካም ነገር ሁለ አንድ ነገር እንኳን ሳይፈጸም አልቀረም፡፡

ሃሳቡን ለማጉላት ይህ የተገለጸው በአሉታ ነው፡፡ "ያህዌ ለእስራኤል ቤት የተናገረው እያንዳንዱ መልካም ቃል ኪዳን ተፈጸመ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ምፀት/ላይዶክስ የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 22

1 በዚያን ጊዜም ኢያሱ የሮቤል ልጆችንና የጋድ ልጆችን የምናሴንም ነገድ እኩሌታ ጠራቸው። 2 እንዲህም አላቸው፦ የእግዚእአብሔር አገልጋይ ሙሴ ያዘዛችሁን ሁሉ ጠብቃችኋል፥ እኔም ላዘዝኋችሁ ነገር ሁሉ ታዝዛችኋል። 3 ይህንም ያህል ብዙ ጊዜ እስከ ዛሬ ድረስ ወንድሞቻችሁን አልተዋችሁም፥ የአምላካችሁንም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ጠብቃችኋል። 4 አሁንም እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ተናገራቸው ወድሞቻችሁን አሳርፎአቸዋል። አሁን እንግዲህ ተመለሱ፥ ወደ ቤታችሁና የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ በዮርዳኖስ ማዶ ወደ ሰጣችሁ ወደ ርስታችሁ ምድር ሂዱ። 5 የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴ ያዘዛችሁን ትእዛዙንና ሕጉን ታደርጉ ዘንድ እግዚአብሔር አምላካችሁን ትወድዱ ዘንድ መንገዱንም ሁሉ ትሄዱ ዘንድ፥ ትእዛዙንም ትጠብቁ ዘንድ፥ ወደ እርሱም ትጠጉ ዘንድ፥ በፍጹምም ልባችሁ በፍጹምም ነፍሳችሁ ታመልኩ ዘንድ ብቻ እጅግ ተጠንቀቁ። 6 ኢያሱም መረቃቸው፥ ሰደዳቸውም፤ ወደ ቤታቸውም ሄዱ። 7 ለምናሴም ነገድ እኩሌታ ሙሴ በባሳን ውስጥ ርስት ሰጥቶአቸው ነበር፤ ለቀረው እኩሌታው ግን ኢያሱ በዮርዳኖስ ማዶ በምዕብብ ወንን በወንድሞቻቸው መካከል ርስት ሰጣቸው። ኢያሱም ወደ ቤታቸው በሰደዳቸው ጊዜ 8 እንዲህ ብሎ መረቃቸው፦ በብዙ ብልጥግና በእጅግም ብዙ ከብት፥ በብርም፥ በወርቅም፥ በናስም፥ በብረትም፥ በእጅግም ብዙ ልብስ ወደ ቤታችሁ ተመለሱ፤ የጠላቶቻችሁንም ምርኮ ከወንድሞቻችሁ ጋር ተካፈሉ። 9 የሮቤልም ልጆች የጋድም ልጆች የምናሴም ነገድ እኩሌታ የእስራኤል ሕዝብ በከነዓን በሴሎ ትተው ወደ ቤታቸው ተመለሱ። በሙሴም እጅ በተሰጠ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ወደ ተቀበሉአት ወደ ርስታቸው ወደ ገለዓድ ምድር ይገቡ ዘንድ ሄዱ። 10 በከነዓን ምድር ወዳለው ወደ ዮርዳኖስ አቅራቢያም በመጡ ጊዜ የሮቤል ልጆችና የጋድ ልጆች የምናሴም ነገድ እኩሌታ በዚያ በዩርዳኖስ አጠገብ ታላቅ መሠዊያ ሠሩ። 11 ለእስራኤልም ልጆች፦ እነሆ፥ በከነዓን ምድር ዳርቻ በዮርዳኖስ አጠገብ ባለው ግዛት፥ የእስራኤል ልጆች ባሉበት ወገን፥ የሮቤል ልጆችና የጋድ ልጆች የምናሴም ነገድ እኩሌታ መሠዊያ ሠርውዋል፤ የሚል ወሬ ደረሰላቸው። 12 የእስራኤል ሕዝብ ይህን በሰሙ ጊዜ የእስራኤል ልጆች ማኅበር ሁሉ ወጥተው እነርሱን ሊዋጉ በሴሎ ተሰበስቡ። 13 የእስራኤልም ልጆች በገለዓድ ምድር ወዳሉት ወደ ሮቤል ልጆችና ወደ ጋድ ልጆች ወደ ምናሴም ነገድ እኩሌታ መልእክት ላኩ። የካህኑን የአልዓዛርን ልጅ ፊንሐስን ደግሞ ላኩ፥ 14 ከእርሱም ጋር አሥር አለቆች ነበሩ፥ ከእስራኤል ከነገዱ ሁሉ አንድ አንድ የአባቶች ቤት አለቃ እያንዳንዱም በእስራኤል አእላፋት መካከል የእየአባቶቻቸው ቤት አለቃ ነበሩ። 15 በገለዓድም ምድር ወዳሉት ወደ ሮቤል ልጆችና ወደ ግድ ልጆች ወደ ምናሴም ነገድ እኩሌታ መጡ፥ እንዲህም ብለው ተናገሩአቸው፦ 16 የእግዚአብሔር ማኅበር ሁሉ የሚለው ይህ ነው፦ ይህ በእስራኤል አምላክ ላይ ያደረጋችሁት ኃጢአት ምንድን ነው? ዛሬ እግዚእአብሔርን ከመከተል ተመልሳችኋል ዛሬም በራሳችሁ መሠዊያ በመሥራታችሁ በእግዚአብሔር ላይ ዐምፃችኋል። 17 በፌጎር ያደረገነው ኃጢአታችን አይበቃምን? እስከ ዛሬም ድረስ ከዚያ ኃጢአት ራሳችንን አላነጸንበትም። ከዚያም ኃጢአት የተነሣ በእግዚአብሔር ማኅበር ላይ መቅሠፍት ወረደ። 18 እናንተ ዛሬ እግዚአብሔርን ከመከተል መመለስ ይገባችኋልን? ዛሬ በእግዚአሔር ላይ ብታምፁ ነገ በእስራኤል ማኅበር ሁሉ ላይ ይቆጣል። 19 የርስታችሁም ምድር የረከሰ ቢመስላችሁ የእግዚአብሔር ማደሪያ ወደ ሚቀመጥበት ወደ እግዚአብሔር ርስት ምድር አልፋችሁ በመካከላችን ውረሱ። ከአምላካችንም ከእግዚአብሔር መሠዊያ ሌላ ለእናንተ መሠዊያ በመሥራታችሁ በእግዚአብሔርና በእኛ ላይ አታምፁ። 20 የዛራ ልጅ አካን እርም ነገር በመውሰድ ኃጢአትን ስለ ሠራ በእስራኤል ማኅበር ሁሉ ላይ ቁጣ አልወረደምን? እርሱም በኃጢአት ብቻውን አልሞተም። 21 ከዚያም የሮቤል ልጆችና የጋድ ልጆች የምናሴም ነገድ እኩሌታ ለእስራኤል አለቆች እንዲህ ብለው መለሱላቸው፦ 22 ሁሉን የሚችል አምላክ እግዚአብሔር ታላቁ አምላክ እግዚአብሔር እርሱ ያውቃል፥ እስራኤልም እንዲያውቅ ያደርጋል! በእግዚአብሔር ላይ ዐምፀንና ተላልፈን እንደ ሆነ ዛሬ አታድነን እግዚአሔርን ከመከተል እንድንመለስ፥ የሚቃጠለውን 23 መሥዋዕትና የእህልን ቁርባን እንድናሳርግበት፥ የደኅነትትንም መሥዋዕት እንድናቀርብበት ብለን መሠዊያ ሠርተን እንደ ሆነ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ ይበቀለን። 24 ይልቁንም ከልባችን ፍርሃት የተነሣ፦ በሚመጣው ዘመን ልጆቻችንን፦ እናንተ የሮቤልና የጋድ ልጆች፥ ከእስራኤል አምላክ ከእግዚአብሔር ጋር ምን አላችሁ? 25 እግዚአብሔር በእኛና በእናንተ መካከል ዮርዳኖስን ድንበር አድርጎአል። እናንተ የሮቤልና የጋድ ልጆች በእግዚአብሔር ዘንድ እድል ፈንታ የላችሁም ይሉአቸዋል ብለን ይህን አደረግን። በዚህም ልጆቻችሁ ልጆቻችንን እግዚአብሔርን ከመፍራት ያስተዋቸዋል። 26 ስለዚህ፦ መሠዊያ እንሥራ አልን፤ ነገር ግን ለሚቃጠል መሥዋዕት ወይም ለሌላ መሥዋዕት አይደለም፤ 27 ነገር ግን በእኛና በእናንተ መካከል ከእኛም በኋላ በትውልዳችንና በትውልዳችሁ መካከል በሚቃጠል መሥዋዕትና በቁርባን በደኅንነትም መሥዋዕታችን እግዚአብሔርን እናመልክ ዘንድ በሚመጣውም ዘመን ልጆቻችሁ ልጆቻችንን፦በእግዚአብሔር ዘንድ እድል ፈንት የላችሁም እንዳይሉ ምስክር ይሆናል። 28 ስለዚህም አልን፦ በሚመጣው ዘመን ለእኛ ወይም ለትውልዳችን፥ ይህን እንላለን እኛ፦ እነሆም አባቶቻችን ያደረጉትን የእግዚአብሔርን መሠዊያ ምሳሌ እዪ በእኛና በእናንተ መካከል ምስክር ነው እንጂ ስለሚቃጠል መሥዋዕታችን ስለሌላ መሥዋዕት አይደለም። በማደሪያው ፊት ካለው ከአምላካችን 29 ከእግዚአብሔር መሠዊያ ሌላ ለሚቃጠል መሥዋዕትና ለእህል ቁርባን ለሌላ መሥዋዕትም የሚሆን መሠዊያን የሠራነው በእግዚአብሔር ላይ በማመፅ እግዚአብሔርንም ዛሬ መከተልን ለመተው በማለት እንደ ሆነ ይህ ከእኛ ይራቅ። 30 ካህኑ ፊንሐና የማኅበሩ አለቆች፥ ከእርሱ ጋር ከነበሩት የእስራኤል አለቆች፥ የሮቤል ልጆችና የጋድ ልጆች የምናሴም ልጆች የተናገሩትን ቃል በሰሙ ጊዜ ነገሩ እጅግ ደስ አሰኛቸው። 31 የካህኑም በአልዓዛር ልጅ ፊንሐስ ለሮቤል ልጆችና ለጋድ ልጆች ለምናሴም ልጆች፦ ይህን መተላለፍ በእግዚአብሔር ላይ አላደረጋችሁምና እግዚአብሔር በመካከላችን እንዳለ ዛሬ እናውቃለን፤ አሁን የእስራኤልን ልጆች ከእግዚአብሔር እጅ አድናችኋል አላቸው። 32 የካህኑም የአልዓዛር ልጅ ፊንሐስና አለቆቹ ከሮቤል ልጆችና ከጋድ ልጆች ዘንድ ከገለዓድ አገር ወደ ከነዓን አገር ወደ እስራኤል ልጆች ተመለሱ፥ ወሬም አመጡላቸው። 33 ነገሩም የእስራኤል ልጆችን ደስ አሰኘ፤ የእስራኤልም ልጆች እግዚአብሔርን አመሰገኑ፥ ከዚያም ወዲያ የሮቤል ልጆችና የጋድ ልጆች የተቀመጡባትን ምድር ያጠፉ ዘንድ ወጥተው አንዲወጉአቸው አልተናገሩም። 34 የሮቤል ልጆችና የጋድ ልጆች፦ እግዚአብሔር አምላክ እንደ ሆነ ይህ በመካከላችን ምስክር ነው ሲሉ መሠዊያውን ምስክር ብለው ጠሩት።



Joshua 22:1

ሮቤላውያን

የሮቤል ነገድ ሰዎች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ጋዳውያን

የጋድ ነገድ ሰዎች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ድምጼን ታዛችኋል

እዚህ ስፍራ "ድምጼ" የሚለው የሚያመለክተው ኢያሱ የተናገራቸውን ነገሮች ነው፡፡ "የተናገርኩትን ሁሉ ታዛችኋል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት)

ወንድሞቻችሁን አልተዋችሁም

ይህ በአዎንታዊ መልክ ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ከወንድሞቻችሁ ጋር ቆይታችኋል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ምፀት/ላይዶክስ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:4

በመንገዱ ሁሉ ለመሄድ

ያህዌን የሚታዘዝ ሰው በያህዌ መንገዶች ወይም ጎዳናዎች እንደሄደ ተደርጎ ይነገራል፡፡ "እርሱ ያለውን ነገር ሁሉ መታዘዝ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በሙሉ ልባችሁ እና በሙሉ ነፍሳችሁ

"ልብ" እና "ነፍስ" የሚሉት ቃላት እዚህ ስፍራ ላይ ያገለገሉት የሰውን ሁለንተና ለመግለጽ ነው፡፡ "በሙሉ ሃሳባችሁ እና ስሜታችሁ" ወይም "በሁለንተናችሁ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:7

የዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው

ብረት

ጠንካራ፣ ከባድ፣ ማግኔት የሚስበው ነገር

ምርኮ/ዘረፋ

ያሸነፈው ሰራዊት ካሸነፈው ህዝብ ዋጋ ያለውን ማናቸውንም ነገር ይወስዳል

Joshua 22:9

በሙሴ እጅ የያህዌ ትዕዛዝ

"በእጅ" የሚለው ሀረግ ያህዌ ትዕዛዙን ለመስጠት/ለማቅረብ ሙሴን እንደተጠቀመበት የሚገልጽ ፈሊጣ አነጋገር ነው፡፡ "ያህዌ ያዛችሁ ዘንድ ሙሴን ተናገረው/ አዘዘው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:10

የዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው

ከከነዓን ምድር ፊት

ከዮርዳኖስ ወንዝ ባሻገር የሚኖሩ እስራኤላውያን ነገዶች መሰዊያውን ወደ ገነቡበት ከነዓን ይገባሉ፡፡ ይህ ስፍራ የተገለጸው ሌሎች ነገዶች የሚኖሩበት የከነዓን "ፊት " ወይም "መግቢያ" እንደነበረ ተደርጎ ነው፡፡ "ወደ ከነዓን ምድር መግቢያ ላይ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ገሊሎት

የከተማ ስም (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:12

ጦርነት

በሁለት አገራት ወይም ህዝቦች መሃል በጦር ትጥቅ የሚደረግ ግጭት

Joshua 22:13

አልዓዛር

የወንድ ስም (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:15

መላው የያህዌ ጉባኤ ይህንን ተናገረ

መላው የእስራኤል ህዝብ በአንድነት የተገለጸው በነጠላ ቁጥር አንድ ሰው እንደሆኑ ተደርጎ ነው፡፡ "ሌሎቹ እስራኤላውያን ሁሉ ይጠይቃሉ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡

Joshua 22:17

በፌጎር የሰራነው ኃጢአት አይበቃንምን?

ይህ ጥያቄ የቀድሞ ኃጢአታቸው ምን ያህል የከፋ እንደሆነ አጉልቶ ያሳያል፡፡ ይህ በዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "አስቀድመን በፌጎር እጅግ ክፉ ኃጢአት ሰርተናል!" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ፌጎር

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ በኢያሱ 13፡20 ላይ በተረጎሙት መንገድ ይተርጉሙት፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ አሁን ድረስ እንኳን ራሳችንን ከዚያ አላነጻንም

ይህ በአዎንታዊ መልክ ሊጻፍ ይችላል፡፡ "እስከ አሁን ድረስ በዚያ ኃጢአት ውስጥ እንገኛለን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ምፀት/ላይዶክስ የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ ዛሬ ድረስ ያህዌን ከመከተልስ መራቅ ነበረባችሁን?

ይህ ጥያቄ ህዝቡን በኃጢአቱ ለመገሰጽ ውሏል፡፡ ይህ በዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ዛሬ ያህዌን ከመከተል መራቅ የለባችሁም!" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:19

አካን…ዛራ

የወንዶች ስሞች ናቸው (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የዛራ ልጅ አካን ለእግዚአብሔር የተለዩ ነገሮችን በመንካት/በመውሰድ እምነትን አላጎደለምን?በመላው የእስራኤል ህዝብ ላይ ቁጣ አልወረደምን?

እነዚህ ጥያቄዎች ህዝቡ ባለፊት ኃጢአቶች ስለደረሰበት ቅጣት ለማስታወስ ውለዋል፡፡ እነዚህ ጥያቄዎች በዐፍተ ነገር ሊገለጹ ይችላሉ፡፡ "የዛራ ልጅ አካን ለእግዚአብሔር የተለዩ ነገሮችን በመንካት ኃጢአት ሰርቷል፡፡ ደግሞም በዚያ ምክንያት እግዚአብሔር መላውን የእስራኤል ህዝብ ቀጥቷል!" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:21

ይህ የሆነው በአመጽ ከሆነ.. ያህዌ ለዚህ ስራችን ይቅጣን

ሶስቱ ነገዶች የቀረበባቸው እውነት ላለመሆኑ ሁለት መላምታዊ ሃሳቦችን አቅርበዋል፡፡ ሌሎች አማልክትን ለማምለክ መሰዊያ አላበጁም፡፡ (መላምታዊ ሁኔታዎች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:24

አጠቃላይ መረጃ፡

የሮቤል ነገድ፣ የጋድ እና የምናሴ ነገድ እኩሌታ መልሳቸውን ሰጡ፡፡

የእናንተ ልጆች ለልጆቻችን እንዲህ ሊሉ ይችላሉ … ከእስራኤል አምላክ ጋር ምን አላችሁ?

ይህ ሶስቱ ነገዶች የሌሎች ነገዶች ልጆች ወደ ፊት ሊያደርጉት ይችላሉ ብለው ያሰቡት መላምታዊ ክስ ነው፡፡ (መላምታዊ ሁኔታዎች የሚለውን ይመልከቱ)

ከእስራኤል አምላክ ከያህዌ ጋር ምን አላችሁ?

ሶስቱ ነገዶች ይህንን ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የተጠቀሙት ሊያስወግዱት የሚፈልጉትን ሁኔታ አጉልተው ለማሳየት ነው፡፡ ይህ በዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "ከእስራኤል አምላክ ከያህዌ ጋር አንዳች የላችሁም!" (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:25

አጠቃላይ መረጃ፡

የሮቤል ነገድ፣ የጋድ እና የምናሴ ነገድ እኩሌታ መልሳቸውን መስጠት ቀጠሉ፡፡

ያህዌ ዮርዳኖስን… አድርጓልና ከያህዌ ጋር አንዳች የላችሁም

ይህ ሶስቱ ነገዶች የሌሎቹ ነገዶች ልጆች ወደ ፊት ሊያደርጉት ይችላሉ ብለው ያሰቡት የመላምታዊ ክሱ ቀጣይ ነው፡፡ (መላምታዊ ሁኔታዎች የሚለውን ይመልከቱ)

የዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው ስለዚህ የእናንተ ልጆች የእኛን ልጆች ያህዌን ከማምለክ እንዲያቆሙ ሊያደርጉ ይችላሉና ሶስቱ ነገዶች መሰዊያ የገነቡት ለወደፊት ይህ መላምታዊ ሁኔታ እንዳይፈጠር ለማስወገድ ነው፡፡ (መላምታዊ ሁኔታዎች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:26

አጠቃላይ መረጃ፡

የሮቤል ነገድ፣ የጋድ እና የምናሴ ነገድ እኩሌታ አሁን መልሳቸውን ሰጡ፡፡

በእናንተ እና በእኛ መሃል ምስክር እንዲሆን

መሰዊያው የተገለጸው ለሶስቱ ነገዶች መብቶች ማስረጃ መስጠት የሚችል ምስክር እንደሆነ ተደርጎ ነው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ስለዚህም የእናንተ ልጆች በሚመጣው ዘመን ለእኛ ልጆች በፍጹም "ከያህዌ ዘንድ አንዳች ድርሻ የላችሁም" ሊሏቸው አይችሉም

ይህ ሶስቱ ነገዶች እንዲሆን የማይሹት መላምታዊ ሁኔታ ነው፡፡ (መላምታዊ ሁኔታዎች የሚለውን ይመልከቱ)

አንዳች ድርሻ

"ምንም ክፍል" ወይም "ምንም ርስት"

Joshua 22:28

አጠቃላይ መረጃ፡

የሮቤል ነገድ፣ የጋድ እና የምናሴ ነገድ እኩሌታ አሁን መልሳቸውን ሰጥተው አበቁ፡፡

ይህ መነገር ካለበት… በእኛ እና በእናንተ መሃል ምስክሩ

ሶስቱ ነገዶች በቀረበባቸው ክስ በመጪው ዘመን ሊሆንም ላይሆንም ስለሚችለው ያላቸውን መልስ እየሰጡ ነው፡፡ (መላምታዊ ሁኔታዎች የሚለውን ይመልከቱ)

አመጽ ከእኛ ይራቅ

የማመጽ ሃሳብ እንደሌላቸው ይህ ሃሳብ የተገለጸው፣ ከእነርሱ በጣም በሩቅ ስፍራ ላይ እንደሚገኝ ነገር ተደርጎ ነው፡፡ "እኛ በእርግጥ አናምጽም" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እርሱን ከመከተል ርቃችኋል

ያህዌን መከተልን ማቆም የተገለጸው እነርሱ ከእርሱ እንደዞሩ ተደርጎ ነው፡፡ "እርሱን መከተል አቆሙ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 22:30

ቃሎቹን ሰሙ

"መልዕክቱን ሰሙ" በዐይኖቻቸው ፊት መልካም ነበር እዚህ ስፍራ "በዐይኖቻቸው ፊት" የሚለው "በእነርሱ አስተያየት" ማለት ነው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በእርሱ ላይ ይህንን ክህደት መፈጸም

"ለእርሱ የገባችሁትን ቃል ኪዳን ማፍረስ"

እናንተ የእስራኤልን ህዝብ ከያህዌ እጅ አድናችኋል

እዚህ ስፍራ "የያህዌ እጅ" የሚለው የሚያመለክተው ቅጣትን ነው፡፡ ህዝቡን መጠበቅ የተገለጸው ከእርሱ እጅ እንደ ማዳን ተደርጎ ነው፡፡ "ያህዌ እኛን እንዳይቀጣን ጠብቃችሁናል" (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት)

Joshua 22:32

የተናገሩት በህዝቡ ዐይን ደስ የሚያሰኝ ሆነ

እዚህ ስፍራ "በዐይኖች ፊት ደስ የሚያሰኝ" የሚለው "ተቀባይነት አገኘ" ማለት ነው፡፡ "ህዝቡ የሽማግሌዎቹን ንግግር ተቀበለ"በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ምድሪቱን ማጥፋት

"በምድሪቱ የሚገኘውን ማናቸውንም ነገር ማጥፋት"

Joshua 22:34

እንዲህ አሉ

ይህ የሚያመለክተው ሮቤላውያንን እና ጋዳውያንን ነው

ይህ በመሃላችን ምስክር ነው

መሰዊያው የተነገረው የሶስቱ ነገዶች ማረጋገጫ ምስክር እንደሆነ ነው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 23

1 ከብዙ ቀናት በኋላ፥እግዚአብሔርም እስራኤልን በዙሪያቸው ካሉት ጠላቶቻቸው ሁሉ ካሳረፈ፥ ኢያሱ ሸምግሎ ነበር። 2 ኢያሱም እስራኤልን ሁሉ ሽማግሌዎቻቸውን፥ አለቆቻቸውን፥ ፈራጆቻቸውንና ሹማምቶቻቸውን ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ እኔ በጣም ሸምግያለሁ። 3 እናንተም አምላካችሁ እግዚአብሔር በእነዚህ አሕዛብ ሁሉ ስለ እናንተ ያደረገውን ሁሉ አይታችኋል፤ ስለ እናንተ የተዋጋ እርሱ አምላካችሁ እግዚአብሔር ነው። 4 ተመልከቱ! እኔ ካጠፋኋቸው አሕዛብ ሁሉ ጋር ከዮርዳኖስ ጀምሮ እስካለው እስከ ታላቁ ባሕር ድረስ ለነገዶቻችሁ ርስት እንዲሆኑ መድቤላችኋለሁ። 5 እግዚአሔር አምላካችሁም እርሱ ከፊታችሁ በብርቱ ይበትናቸዋል፥ ከፊታችሁም ያሳድዳቸዋል። እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ተናገራችሁም ምድራቸውን ትወርሳላችሁ። 6 ስለዚህም በሙሴ ሕግ መጽሐፍ የተጻፈውን ሁሉ ለመጠበቅና ለማድረግ በጣም በርቱ፥ ከእርሱም ወደ ቀኝም ወደ ግራም ፈቀቅ አትበሉ። 7 በእናንተ መካከል ወደ ቀሩት ወደ እነዚህ አሕዛብ አትግቡ፤ የአማልክታቸውንም ስም አትጥሩ፥ አትማሉባቸውም፥ አታምልኩአቸውም፥ አትስገዱላቸውም። 8 እስከ ዛሬ ድረስ እንዳደረጋችሁት በእግዚአብሔር በአምላካችሁ ተጣበቁ። 9 እግዚአብሔርም ታላላቆችንና ኃይለኞችን መንግሥታት ከፊታችሁ አስወጣላችሁ። እስከ ዛሬም ድረስ ማንም ሊቋቋማችሁ አልቻለም። 10 እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ተጋገራችሁ ስለ እናንተ የሚዋጋ እርሱ ነውና፥ ከእናንተ አንድ ሰው ሺህ ሰውን ያሳድዳል። 11 እግዚእብሔር አምላካችሁን ትወድዱት ዘንድ ትኩረት አድርጉ። 12 እናንተ ግን ተመልሳችሁ በመካከላችሁ ከቀሩት ከእነዚህ አሕዛብ ጋር ብትጣበቁ፥ወይም ከእነርሱም ጋር ብትጋቡ፥ ወይም እናንተ ወደ እነርሱም ወደ እናንተ ኅብረት ብታደርጉ፥ 13 ከዚያም እግዚአብሔር አምላካችሁ ከመካከላችሁ እነዚህን ሰዎች እንደማያስወጣችሁ በርግጥ እወቁ። በዚህ ፈንታ ከዚህች እግዚአብሔር ከሰጣችሁ ከመልካሚቱ ምድር እስክትጠፉ ድረስ ለእናንተም መውደቂያና ወጥመድ፥ በጎናችሁም መግረፊያ፥ በዓይናችሁም እሾህ ይሆኑባችኋል። 14 እነሆም ዛሬ የምድርን መንገድ ሁሉ እሄዳለሁ፤ እናንተም እግዚአብሔር ስለ እናንተ ከተናገረው ከመልካም ነገር ሁሉ አንድ ነገር እንዳልቀረ በልባችሁ ሁሉ በነፍሳችሁም ሁሉ እወቁ፥ ሁሉ ደርሶላችኋል፤ ከእርሱም አንድ ነገር አልቀረም። 15 እግዚአብሔ አምላካችሁ የተናገረው መልካም ነገር ሁሉ እንደ ደረሰላችሁ፥ እግዚአብሔር አምላካችሁ ከሰጣችሁ ከዚህች ከመልካሚቱ ምድር እናንተን እስኪያጠፋችሁ ድረስ እግዚአብሔር እንዲሁ ክፉን ነገር ሁሉ ያመጣባችኋል። 16 የእግዚአብሔር አምላካችሁን ቃል ኪዳን ብታፈርሱ፥ ሄዳችሁም ሌሎችን አማልክት ብታመልኩ፥ ብትሰግዱላቸውም፥ በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር ቁጣ ይነድድባችኋል፥ ከሰጣትችሁም ከመልካሚቱ ምድር ፈጥናችሁ ትጠፋላችሁ።



Joshua 23:1

በጣም አረጀ

ለብዙ አመታት የኖረ

Joshua 23:4

የዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው

በምዕራብ

ይህ የሚያመለክተው ፀሐይ የምትጠልቅበትን አቅጣጫ ነው

Joshua 23:6

ከዚህ ወደ ቀኝ ወይም ወደ ግራ ዞር ማለት

የሙሴን ትዕዛዛት አለመጠበቅ የተገለጸው ከዚህ መንገድ ወደ ቀኝ ወይም ወደ ግራ ዞር ማለት ተብሎ ነው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

አትቀላቀሉም

ሊሰጡ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ከእነርሱ ጋር የቀረበ ወዳጅነት መመስረት 2) ከእነርሱ ጋር በጋብቻ መተሳሰር

መጥቀስ

መናገር

አማልዕክቶቻቸው

ይህ የሚያመለክተው የሌሎችን ህዝቦች አማልዕክት ነው

ያህዌን አጥብቆ መያዝ

"ያህዌን አጥብቆ መያዝ፡፡" በያህዌ ማመን የተገለጸው እርሱን አጥብቆ እንደመያዝ ተደርጎ ነው፡፡ "በያህዌ ማመንን መቀጠል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

እስከ ዛሬ ድረስ

"እስከ ዛሬ ዘመን ድረስ"

Joshua 23:9

በፊትህ ለመቆም

እዚህ ስፍራ "መቆም" የሚለው የሚወክለው በጦርነት ውስጥ ስፍራ/ምድር መያዝን ነው፡፡ "አንተ" የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእስራኤልን መላ ህዝብ ነው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት እና አንተ የሚለው ቃል ልዩ ልዩ መልኮች የሚሉትን ይመልከቱ)

ነጠላ

አንድ ብቻ

አንድ ሺህ

"1,000" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 23:12

ከእነዚህ ህዝቦች ትሩፋን ጋር የጠበቀ ግንኙነት መመስረት

የእነዚህን ህዝቦች እምነቶች መቀበል የተገለጸው እነርሱን ጋር አጥብቆ መያዝ ተደርጎ ነው፡፡ "የእነዚህን ህዝቦች እምነቶች መቀበል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

መሰናክል/አሽክላ እና ወጥመድ

"መሰናክል" እና "ወጥመድ" የሚሉት ቃላት በመሰረቱ ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፡፡ ቃላቱ በአንድነት የሚናገሩት ሌሎች ህዝቦች ለእስራኤል ከፍተኛ ችግር እንደሚሆኑ ነው፡፡ (ጥንድ ትርጉም እና ዘይቤያዊ አነጋገር የሚሉትን ይመልከቱ)

ለጀርባችሁ ጅራፍ እና ለዐይኖቻችሁ እሾህ

እነዚህ ሀረጋት የሚናገሩት እነዚህ ህዝቦች በእስራኤል ላይ የሚፈጥሩት ችግር የጅራፍ እና የእሾህ ያህል የሚያሰቃያቸው መሆኑን ነው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 23:14

የምድርን ሁሉ መንገድ ልሄድ ነው

ኢያሱ ሞቱን ለመናገር ትሁት አገላለጽ ይጠቀማል፡፡ "መሞቴ ነው/ልሞት ነው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዩፊሚዝም/ጸያፍ ወይም አስነዋሪ ቃልን ሻል ባለ ቃል መጠቀም)

በሙሉ ልባችሁ እና ነፍሳችሁ ታውቃላችሁ

እዚህ ስፍራ "ልቦች" እና "ነፍሶች" የሚሉት ቃላት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፡፡ቃላቱ በአንድነት ሆነው ጠለቅ ያለ ግላዊ እውቀትን ያጎላሉ፡፡ (ጥንድ ትርጉም የሚለውን ይመልከቱ)

አንድ ቃል እንኳን ሳይፈጸም አልቀረም

እነዚህ ቃላት የያህዌ ቃል ኪዳኖች ሁሉ መፈጸማቸውን ትኩረት ሰጥተው ይገልጻሉ፡፡ ይህ በአዎንታዊ ዐረፍተ ነገር ሊጻፍ ይችላል፡፡ "እያንዳንዱ ቃል ተፈጸመ/እውን ሆነ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ድርብ አሉታ እና ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 23:16

ይህንን ያደርጋል

ይህ በቀደመው ቁጥር ውስጥ የተጠቀሰውን ቅጣት አስፈሪነት ያመለክታል

ሌሎችን አማልዕክት ማምለክ እና ለእነርሱ መስገድ

እነዚህ ሁለት ሀረጋት በመሰረቱ ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፡፡ ሁለተኛው ህዝቡ እንዴት "ሌሎችን አማልክት እንደሚያመልክ" ይገልጻል፡፡" (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

የያህዌ ቁጣ በእናንተ ላይ ይነዳል

በዚህ ስፍራ "ይነዳል" የሚለው ቃል፣ ልክ እሳት "እንደሚቀጣጠል" ወይም "በመቀጣጠል" እንደሚጀምር፣ ወይም ደረቅ ሳርን/ጭድን ወይም ጭራሮን ማቃጠል መጀመር ቀላል የሆነውን ያህል የያህዌ ቁጣ ለመጀመሩ ዘይቤያዊ አነጋገር ነው፡፡ "ያህዌ በእናንተ መቆጣት ይጀምራል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)


Chapter 24

1 ኢያሱም የእስራኤልን ነገድ ሁሉ ወደ ሴኬም ሰበስበ፥ የእስራኤልንም ሽማግሌዎችን፥ አለቆቻቸውን፥ ፈራጆቻቸውንና ሹማምቶቻቸውን ጠራቸው፤ እነርሱም በእግዚአብሔር ፊት ቆሙ። 2 ኢያሱም ለሕዝቡ ሁሉ እንዲህ አለ፦ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ አባቶቻችሁ፥ የአብርሃምና የናኮር አባት ታራ፥ አስቀድመው በወንዝ ማዶ ተቀመጡ፤ ሌሎችንም አማልክት አመለኩ። 3 አባታችሁንም አብርሃምን ከኤፍራጥስ ወንዝ ማዶ ወስጄ በከነዓን ምድር ሁሉ መራሁት፤ ዘሩንም በልጁ በይስሐቅ በኩል እንዲበዛ ሰጠሁት። 4 ለይስሐቅም ያዕቆብንና ዔሳውን ሰጠሁት። ለዔሳውም የሴይርን ተራራ ርስት አድርጌ ሰጠሁት፥ ነገር ግን ያዕቆብና ልጂቹ ወደ ግብፅ ወረዱ። 5 ሙሴንና አሮንንም ላክሁ፥ ግብፃውያንን በመቅሠፍት መታሁ። ከዚያም በኋላ አወጣኋችሁ። 6 አባቶቻችሁንም ከግብፅ አወጣኋችው፤ ወደ ባሕሩም መጣችሁ። ግብፃውያንም አባቶቻችሁን በሰረገሎችና በፈረሰኞች እስከ ኤርትራ ባሕር ድረስ አሳደዱአቸው። 7 አባቶቻችሁም ወደ እግዚአብሔር በጮኹ ጊዜ በእናንተና በግብፃውያን መካከል ጨለማ አደረገ። ባሕሩንም በእነርሱ ላይ መለሰባቸው፥ አሰጠማቸውም። ዓናኖቻችሁም በግብፃውያን ላይ ያደረግሁትን አይታችኋል። ለረጅም ጊዜም በምድረ በዳ ተቀመጣችሁ። 8 እኔም በዮርዳኖስ ማዶ ወደ ተቀመጡበት ወደ አሞራውያን ምድር አመጣኋችሁ። ከእናንም ጋር ተዋጉ፥ በእጃችሁ አሳልፌ ሰጠኋችሁ። ምድራቸውንም ወረሳችሁ፤ ከፊታችሁም አጠፋኋቸው። 9-10 የሞዓብም ንጉሥ የሴፎር ልጅ ባላቅ ተንሥቶ ከእስራኤል ጋር ተዋጋ እንዲረግማችሁም የቢዖርን ልጅ በለዓምን ልኮ አስጠራው።እኔ ግን በለዓምን አልሰማሁትም። እርሱም በዚህ ፈንታ ባረካችሁ፥ እኔም ከእጁ አዳንኋችሁ። 11 ዮርዳኖስንም ተሻግራችሁ፥ ወደ ኢያሪኮም መጣችሁ። የኢያሪኮም ሰዎች፥ ከአሞራዊውያን፥ ከፌርዛዊውያን፥ ከከነዓናዊውያን፥ ከኬጢያዊውያን፥ ከጌርጌሳዊውያን፥ ከኤዊያዊውያንና ከኢያቡሳዊውያን፥ ጋር ተዋጉአችሁ። በእነርሱም ላይ ድልን ሰጠኋችሁ፤አሳልፌም በእጃችሁ ሰጠኋችሁ። 12 በፊታችሁ ያሉትን ሁለቱን የአሞራውያንን ነገሥታት እንዲያስወጡአቸው በፊታችሁም ተርብን ሰደድሁባቸው። ይህም በእናንተ ሰይፍና ቀሥት አይደለም። 13 ያልደከማችሁበትንም ምድር፥ ያልሠራችኋቸውንም ዛሬ የተቀመጣችሁባቸውን ከተሞች ሰጠኋችሁ። ያልተከላችኋቸውን ወይንና ወይራ በላችሁ። 14 አሁንም እግዚአብሔርን ፍሩ፥ በፍጹም ቅንነትና ታማኝነት አምልኩት፤ አባቶቻችሁም በኤፍራጥስ ወንዝ ማዶ በግብፅም ያመለኩአቸውን አማልክት ከእናንተ አርቁ፤ እግዚአብሔርንም አምልኩ። 15 እግዚአብሔርንም ማምለክ ክፉ መስሎ ቢታያችሁ፥ እባቶቻችሁ በኤፍራጥስ ወንዝ ማዶ ሳሉ ያመለኩአቸውን አማልክት ወይም በምድራቸው ያላችሁባቸውን የአሞራውያንን አማልክት ታመልኩ እንደ ሆነ፥ የምታመልኩትን ዛሬ ምረጡ። እኔና ቤተ ሰቦቼ ግን እግዚአብሔርን እናመካለን። 16 ሕዝቡም መልሰው እንዲህ አሉ፦ እግዚአብሔርን ትተን ሌሎች አማልክትን ማምለክ ከእኛ ይራቅ፥ 17 እኛንና አባቶቻችንን ከባርነት ቤት ከግብፅ ምድር ያወጣን፥ በዓይናችንም ፊት እነዚያን ታላላቅ ተአምራት ያደረገ፥ በሄድንባትም መንገድ ሁሉ ባለፍንባችውም አሕዛብ ሁሉ መካከል የጠበቀን፥ እርሱ አምላካችን እግዚአብሔር ነው። 18 እግዚአብሔር አሕዛብን ሁሉ በምድሪቱም የተቀመጡትን አሞራውያን ከፊታችን አስወጣ። ስለዚህ እርሱ አምላካችን ነውና፤ እግዚአብሔርን እናመልካለን። 19 ኢያሱም ሕዝቡን እንዲህ አላቸው፦ እርሱ ቅዱስና፥ ቀናተኛ አምላክ ነውና፥ እግዚአብሔርን ማምለክ አትችሉም፤ መተላለፋችሁንና ኃጢአታችሁን ይቅር አይልም። 20 እግዚአብሔርን ትታችሁ እንግዶችን አማልክት ብታመልኩ፥ ተመልሶ ክፉ ነገር ያደርግባችኋል፥ መልካም ካደረገላችሁ በኋላ ያጠፋችኋል። 21 ሕዝቡም ኢያሱን፦ እንዲህ አይሁን እግዚአብሔርን እናመልካለን አሉት። 22 ከዚያም ኢያሱ ሕዝቡን፦ እግዚአብሔርን እንድታመኩት እንደመረጣችሁ በራሳችሁ ላይ ምስክሮች ናችሁ አላቸው። እነርሱም፦ ምስክሮች ነን አሉ። 23 እርሱም፦ አሁን እንግዲህ በመካከላችሁ ያሉትን እንግዶችን አማልክት አርቁ፥ ልባችሁንም ወደ እስራኤል አምላክ ወደ እግዚአብሔር አዘንብሉ አላቸው። 24 ሕዝቡም ኢያሱን፦ አምላካችንን እግዚአብሔርን እናመልካለን፥ ድምፁንም እንሰማለን፥ አሉ። 25 በዚያን ቀን ኢያሱ ከሕዝቡ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። በሴምም አዋጅንና ሕግን አደረገላቸው። 26 ኢያሱም እነዚህን ቃላት ሁሉ በእግዚአብሔር ሕግ መጽሐፍ ጻፈ። ታላቁንም ድንጋይ ወስዶ በእግዚአብሔር መቅደስ አጠገብ ከነበረችው ከአድባሩ ዛፍ በታች አቆመው። 27 ኢያሱም ለሕዝቡ፦ ተመልከቱ፥ የተናገረነውን ይህ ድንጋይ ይመሰክርብናል። እግዚአብሔር የተናገርነውን ሁሉ ሰምቶአል። እንግዲህ አምላካችሁን እንዳትክዱ ይህ ምስክር ይሆንባችኋል አላቸው። 28 ስለዚህም ኢያሱ ሕዝቡን ወደ እያንዳንዱ ርስት እንዲሄዱ አደረገ። 29 ከዚህ ነገር በኋላ የእግዚአብሔር አገልጋይ የነዌ ልጅ ኢያሱ ዕድሜው መቶ አሥር ዓመት ሞልቶት ሞተ። 30 በተራራማውም በኤፍሬም አገር በገዓስ ተራራ በሰሜን ባለችው በራሱ ርስት በተምና ሴራ ቀበሩት። 31 ኢያሱ በነረበት ዘመን ሁሉ፤ከኢያሱም በኋላ በነበሩት ለእስራኤልም ያደረገውን የእግዚአብሔርን ሥራ ሁሉ ባወቁት በሽማግሌዎች ዘመን ሁሉ እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አመለኩ። 32 የእስራኤልም ልጆች ከግብፅ የወጡት የዮሴፍን አጥንት ያዕቆብ ከሴም አባት ከኤሞር ልጆች በገዛው እርሻ በሴኬም ቀበሩት። እርሱም በአንድ መቶ ብር ገዛው፤እርሻውም ለዮሴፍ ልጆች ርስት ሆነ። 33 የአሮንም ልጅ አልዓዛር ሞተ፤ በተራራውም በኤፍሬም አገር ለልጁ ለፊንሐስ በተሰጠችው በጊብዓ መሬት ቀበሩት።



Joshua 24:1

ኢያሱ ሁሉንም የእስራኤል ነገዶች ሰበሰበ

ኢያሱ ለነገዶቹ ያደረገው ስብሰባ የተገለጸው ሁሉንም በአንድ ቋት ውስጥ እንዳከማቻቸው ተደርጎ ነው፡፡ "ኢያሱ መላው የእስራኤል ነገድ ከእርሱ ጋር እንዲገኛኝ ጠየቀ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ራሳቸውን ከፊት አቀረቡ

"መጥተው ከፊት ለፊት ቆሙ" ወይም "ከፊት መጡ"

ከረጅም ጊዜ አስቀድሞ

"ከብዙ አመታት በፊት"

ይህ ነው

ኢያሱ ያህዌ አስቀድሞ የተናገረውን መናገር ጀመረ፡፡ ጥቅሱ እስከ ቁጥር 13 መጭሻ ድረስ ይቀጥላል፡፡

ታራ… ናኮር

እነዚህ የወንድ ስሞች ናቸው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 24:3

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ያህዌ እርሱ ከህዝቡ ጋር ስላለው ስምምነት የተናገረውን መጥቀሱን ቀጠለ

ሴይር

የቦት ወይም የስፍራ ስም (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ወረዱ

ግብጽ ከከነዓን ምድር በአቀማመጥ ዝቅ ያለ ነው፡፡ "ተጓዙ"

Joshua 24:5

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ያህዌ እርሱ ከህዝቡ ጋር ስላለው ስምምነት የተናገረውን መጥቀሱን ቀጠለ፡፡

እናነተን አወጣችሁ… አባቶቻችሁን አወጣቸው

ያህዌ በቀጣይነት ስለ ቀደሙትና ስለ አሁኖቹ መላ እስራኤላውያን የሚናገሩትን እነዚህን ሁለት ሀረጎች በመለዋወጥ ይናገራል፡፡ "እናንተ" የሚለው ቃል በዚህ ንግግር ውስጥ ሁሉ ብዙ ቁጥር ሲሆን መላውን የእስራኤል ህዝብ ያመለክታል፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መልኮች/ቅርጾች ይመልከቱ)

Joshua 24:7

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ያህዌ እርሱ ከህዝቡ ጋር ስላለው ስምምነት የተናገረውን መጥቀሱን ቀጠለ፡፡

አባቶቻችሁ… እናንተ

ያህዌ በቀጣይነት ስለ ቀደሙትና ስለ አሁኖቹ መላ እስራኤላውያን የሚናገሩትን እነዚህን ሁለት ሀረጎች በመለዋወጥ ይናገራል፡፡ "እናንተ" የሚለው ቃል በዚህ ንግግር ውስጥ ሁሉ ብዙ ቁጥር ሲሆን መላውን የእስራኤል ህዝብ ያመለክታል፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መልኮች/ቅርጾች ይመልከቱ)

ባህሩ

ይህ የሚያመለክተው ቀይ ባህርን ነው

በምድረበዳ

ሰው የማይኖርበት አካባቢ፣ በረሃ

Joshua 24:8

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ያህዌ እርሱ ከህዝቡ ጋር ስላለው ስምምነት የተናገረውን መጥቀሱን/መናገሩን ቀጠለ፡፡

እናንተ

"እናንተ" የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ሲሆን በእዚህ ንግግር ውስጥ ሁሉ መላውን የእስራኤል ህዝብ ይገልጻል፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መልኮች/ቅርጾች ይመልከቱ)

የዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው

በእጃችሁ አሳልፎ ሰጣቸው

እዚህ ስፍራ "እጅ" የሚለው የሚያመለክተው ሃይልን ነው፡፡ "እንድትማርኳቸው አቅም ሆናችሁ" (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪ በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 24:9

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ያህዌ እርሱ ከህዝቡ ጋር ስላለው ስምምነት የተናገረውን መጥቀሱን/መናገሩን ቀጠለ፡፡

ባላቅ… ሴፎር

የወንዶች ስም (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

እናንተ

"እናንተ" የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ሲሆን በእዚህ ንግግር ውስጥ ሁሉ መላውን የእስራኤል ህዝብ ይገልጻል፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መልኮች/ቅርጾች ይመልከቱ)

እናንተን ከእጁ አዳናችሁ

እዚህ ስፍራ "እጅ" የሚለው የሚያመለክተው ሃይልን ነው፡፡ "እንድትማርኳቸው አቅም ሆናችሁ" (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪ በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 24:11

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ያህዌ እርሱ ከህዝቡ ጋር ስላለው ስምምነት የተናገረውን መጥቀሱን/መናገሩን ቀጠለ፡፡

እናንተ

"እናንተ" የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ሲሆን በእዚህ ንግግር ውስጥ ሁሉ መላውን የእስራኤል ህዝብ ይገልጻል፡፡ (አንተ የሚለውን ቃል መልኮች/ቅርጾች ይመልከቱ)

የዮርዳኖስ

ይህ የዮርዳኖስ ወንዝ አጭር ስያሜ ነው

የተርብ

በአንድነት የምትኖርና በፍጥነት የምትበር ተናዳፊ ትንሽ ነፍሳት፡፡ እዚህ ስፍራ ብዙ "ተርቦች" እንደ አንድ ብቻ ተደርጎ ተገልጽዋል፡፡

Joshua 24:13

አጠቃላይ መረጃ፡

ኢያሱ ያህዌ እርሱ ከህዝቡ ጋር ስላለው ስምምነት የሚናገረውን/የሚጠቅሰውን አጠናቀቀ፡፡

Joshua 24:14

በዐይኖቻችሁ ፊት ስህተት ሆኖ ከታያችሁ

ዐይኖች የሚለው የሚወክለው ማየትን፣ ሲሆን ማየት ደግሞ ሃሳብን ወይም መሻትን ይገልጻል፡፡ "የማትፈልጉ ከሆነ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ቤቴ

ይህ የሚገልጸው በቤቱ የሚኖሩ ቤተሰቦቹን ነው፡፡ "ቤቴ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ ከአንድ ባህሪ በመነሳት ለአንድ ነገር ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 24:16

እኛ… እኛን እና አባቶቻችን

ህዝቡ ከአባቶቻቸው ጋር እንደነበሩ አድርገው ይናገራሉ፣ ደግሞም "እኛን" እና "እኛ" የሚሉት ቃላት "የእኛ አባቶች" ከሚለው ጋር ለዋውጠው ይጠቀማሉ፡፡ (ተውላጠ ስሞች የሚለውን ይመልከቱ)

ከባርነት ቤት

እዚህ ስፍራ "ቤት" የሚለው የባርነታቸውን ስፍራ የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው፡፡ "ባሮች በነበርንበት አገር" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

በውስጣቸው አቋርጠን ባለፍንባቸው አገራት

"እኛ በውስጣቸው ባለፍንባቸው አገሮች"

Joshua 24:19

ህዝቦች

ይህ የሚያመለክው እስራኤላውያንን ነው፡፡

እርሱ ቀናተኛ አምላክ ነው

እግዚአብሔር ህዝቡ እርሱን ብቻ እንዲያመልከው ይፈልጋል

እርሱ ያጠፋችኋል

የያህዌ ቁጣ የተገለጸው እነርሱን እንደሚያጠፋ እስት ሆኖ ነው፡፡ "በእሳት እንደሚያጠፋ እርሱ እናንተን ያጠፋል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 24:21

ህዝቦች

ይህ የሚያመለክው እስራኤላውያንን ነው፡፡

ልባችሁን ወደ ያህዌ መልሱ

ያህዌን ብቻ ለመታዘዝ መወሰን የሚለው የተነገረው ልባቸውን ወደ እርሱ እንደ ማዞር ተደርጎ ነው፡፡ እዚህ ስፍራ "ልብ" የሚለው የሚገልጸው መላ ማንነትን ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ፣ "ልብ" ብዙ ቁጥር ነው፤ ምክንያቱም መላውን እስራኤል እንደ አንድ ቡድን ይገልጻል፡፡ የሆነ ሆኖ፣ "የእናንተ" የሚለው ብዙ ቁጥር እንደመሆኑ ይህንን በብዙ ቁጥር መተርጎሙ እጅግ የተሻለ ይሆናል፡፡ "ራሳችሁን ወደ ያህዌ መልሱ" ወይም "ያህዌን ለመታዘዝ ወስኑ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር፣ ስኔክቲክ/የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ እና አንተ የሚለው ቃል መልኮች/ቅርጾች የሚሉትን ይመልከቱ)

Joshua 24:24

ህዝቦች

ይህ የሚያመለክው እስራኤላውያንን ነው፡፡

እኛ የእርሱን ድምጽ እንሰማለን

እዚህ ስፍራ "መስማት" የሚለው መታዘዝ ማለት ነው፡፡ "እርሱ እንድናደርገው የነገረንን ነገር ሁሉ እንታዘዛለን" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዘይቤያዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

የእግዚአብሔር ህግ መጽሐፍ

ይህ የሙሴ መጽሐፍት ቀጣይ ሊሆን ይችላል፡፡

በዚያ አስቀመጠው

"በዚያ አኖረው/አደረገው"

Joshua 24:27

ህዝቦች

ይህ የሚያመለክው እስራኤላውያንን ነው፡፡

ይህ ድንጋይ ምስክር ይሆናል… ሁሉንም ቃላት ሰምቷል

ኢያሱ ያስቀመጠው ድንጋይ የተገለጸው የተባለውን ሁሉ እንደሰማ እና የተነገረውን ለመመስከር እንደሚችል ሰው ተደርጎ ነው፡፡ (ሰውኛ የሚለውን ዘይቤ ይመልከቱ)

ሆናችሁ አትገኙ

"ሆናችሁ ባትገኙ"

Joshua 24:29

የ110 አመት ሽማግሉ

"የአንድ መቶ አስር አመት ሽማግሌ" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ተምና ሴራ… ገዓስ ተራራ

የቦታ ስሞች (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

Joshua 24:31

ኢያሱ በሕይወት በነበረበት ዘመናት በሙሉ

ይህ የኢያሱን መላ ህይወት የሚያመለክት ፈሊጥ ነው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ኢያሱ ከሞተ በኋላ የኖሩ

"ከኢያሱ በኋላ የኖሩ"

Joshua 24:32

የዮሴፍ አጽም … በሴኬም ቀበሯቸው

የዚህን ዐረፍተ ነገር አጀማመር ስርአት መለወጥ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል፡፡ "የእስራኤል ህዝብ የዮሴፍን አጽም ከግብጽ አውጥተው በሴኬም ቀበሯቸው" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡

አንድ መቶ ሰቅል/ገንዘብ

"100 ሰቅል/ገንዘብ" (ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

አልዓዛር

የወንድ ስም (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

ጊብዓ

የቦታ ስም (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)


Book: Judges


Judges

Chapter 1

1 ከኢያሱ ሞት በኋላ፣ የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሔርን እንዲህ ብለው ጠየቁ፡- “ከነዓናውያንን ለመዋጋት ወደላይ ስንሄድ ማን ይመራናል?” 2 እግዚአብሔርም አላቸው፡- “ይሁዳ ይመራችኋል፡፡ ተመልከቱ፣ ምድሪቱን ለእነርሱ አሳልፌ ሰጥቻለሁ፡፡” 3 የይሁዳም ሰዎች ለወንድሞቻቸው ለስምዖን ሰዎች እንዲህ አሏቸው፡- “ከነዓናውያንን አብረን እንወጋቸው ዘንድ ከእኛ ጋር ለእኛ ወደተሰጠው ክልል ኑ፡፡ እኛም እንዲሁ ለእናንተ ወደተሰጠው ክልል እንመጣለን፡፡” ስለዚህም የስምዖን ነገድ ከእነርሱ ጋር ሄዱ፡፡ 4 የይሁዳ ሰዎችም ወደ ላይ ወጡ፣ እግዚአብሔርም በከነዓናውያንና በፌርዛውያን ላይ ድልን ሰጣቸው፡፡ በቤዜቅም ከእነርሱ አስር ሺህ ሰዎችን ገደሉ፡፡ 5 አዶኒ ቤዜቅን በቤዜቅ አገኙት፣ ከእርሱም ጋር ተዋግተው ከነዓናውያንና ፌርዛውያንን አሸነፉ፡፡ 6 አዶኒ ቤዜቅ ግን ሸሸ፣ ተከታትለውም አገኙትና ያዙት፣ የእጁንና የእግሩን አውራጣቶች ቆረጡ፡፡ 7 አዶኒ ቤዜቅም እንዲህ አለ፡- “የእግርና የእጅ አውራ ጣቶቻቸው የተቆረጠባቸው ሰባ ነገስታት ከእኔ ማዕድ ስር መብላቸውን ሰበሰቡ፡፡ እኔ እንዳደረግሁት፣ እግዚአብሔር በእኔ ላይ አደረገብኝ፡፡” እርሱንም ወደ ኢየሩሳሌም አመጡት፣ በዚያም ሞተ፡፡ 8 የይሁዳ ሰዎች ከኢየሩሳሌም ከተማ ጋር ተዋግተው ተቆጣጠሯት፡፡ በሰይፍ ስለት ወጓት፣ ከተማዋንም አቃጠሏት፡፡ 9 ከዚያም በኋላ የይሁዳ ሰዎች በኮረብታማው አገር ይኖሩ የነበሩትን ከነዓናውያንን ለመዋጋት፣ወደ ኔጌብና ወደ ምዕራቡ ኮረብታ ግርጌ ወረዱ፡፡ 10 ይሁዳም በኬብሮን (የኬብሮን ስም ቀድሞ ቂርያት አርባቅ ትባል ነበር) የሚኖሩትን ከነዓናውያንን ለመውጋት ሄደ፣ ሴሲን፣ አክመንና ቴላሚንም ድል አደረጉ፡፡ 11 ከዚያም የይሁዳ ሰዎች ወደ ዴብር (የዴብር ስም ቀድሞ ቅርያት ሤፍር ተብላ ትጠራ ነበር) ሄዱ፡፡ 12 ካሌብም አለ፣ “ቅርያት ሤፍርን የሚዋጋና የሚቆጣጠራትን ሰው፣ ሴት ልጄን ዓክሳን ሚስት ትሆነው ዘንድ እሰጠዋለሁ፡፡” 13 የካሌብ ታናሽ ወንድም የቄናዝ ልጅ ጎቶንያልም ዴብርን ተቆጣጠረ፣ ስለዚህ ካሌብ ሴት ልጁን ዓክሳን ሚስት ትሆነው ዘንድ ሰጠው፡፡ 14 ዓክሳም ወዲያውኑ ወደ ጎቶንያል መጣች፣ ለእርሱም አባቷ እርሻ እንዲሰጣት እንዲለምነው ጠየቀችው፡፡ ከአሕያዋም በወረደች ጊዜ፣ ካሌብ እንዲህ ብሎ ጠየቃት፣ “ምን እንዳደርግልሽ ትፈልጊያለሽ?” 15 እርሷም እንዲህ አለችው፣ “በረከትን ስጠኝ፡፡ በኔጌብ ምድር ያለውን መሬት ሰጥተኸኛልና፣ የውሃ ምንጭንም ስጠኝ፡፡” ካሌብም የላይኛውንና የታችኛውን ምንጭ ሰጣት፡፡ 16 የቄናዊው የሙሴ አማት ዘሮችም ከባለ ዘንባባዋ ከተማ ለቀው ከይሁዳ ሰዎች ጋር በኔጌብ ወዳለችው ወደ ይሁዳ ምድረ በዳ ከይሁዳ ሰዎች ጋር በዓራድ አጠገብ ለመኖር ሄዱ፡፡ 17 የይሁዳ ሰዎችም ከወንድሞቻቸው ከስምዖን ሰዎች ጋር ሄዱና በጽፋት ይኖሩ የነበሩትን ከነዓናውያንን ወጓቸው፣ፈጽሞም አጠፏት፡፡ የከተማይቱም ስም ሔርማ ይባል ነበር፡፡ 18 በተጨማሪ የይሁዳ ሰዎች ጋዛንና በዙርያዋ ያለውን አገር፣ አስቀሎናንና በዙርያዋ ያለውን አገር እንደዚሁም አቃሮንንና በዙርያዋ ያለውን አገር ሁሉ ተቆጣጠሩ፡፡ 19 እግዚአብሔርም ከይሁዳ ሰዎች ጋር ነበር፣ የኮረብታማውንም አገር ተቆጣጠሩ፣ ነገር ግን በረባዳው ምድር የሚኖሩትን ሰዎች ማስወጣት አልቻሉም ነበር ምክንያቱም ነዋሪዎቹ የብረት ሰረገሎች ነበሯቸው፡፡ 20 ሙሴም እንደተናገረ ኬብሮንን ለካሌብ ሰጡት፣ እርሱም የዔናቅን ሶስት ልጆች ከዚያ አስወጣቸው፡፡ 21 ነገር ግን የቢንያም ሰዎች በኢየሩሳሌም የሚኖሩ ኢያቡሳውያንን አላስወጧቸውም፡፡ ስለዚህ ኢያቡሳውያን እስከዛሬ ድረስ ከቢንያም ሰዎች ጋር በኢየሩሳሌም ይኖራሉ፡፡ 22 የዮሴፍ ወገንም ቤቴልን ለመውጋት ተዘጋጁ፣ እግዚአብሔርም ከእነርሱ ጋር ነበር፡፡ 23 ቀድሞ ሎዛ ተብላ ትጠራ የነበረችውን ቤቴልን ለመሰለል ሰዎችን ላኩ፡፡ 24 ሰላዮቹም ከከተማው አንድ ሰው ሲወጣ አዩ፣ እንዲህም አሉት፣ “ወደ ከተማው እንዴት መግባት እንደምንችል እባክህ አሳየን፣ ለአንተም ቸርነት እናደርግልሃለን፡፡” 25 እርሱም ወደ ከተማው መግቢያውን መንገድ አሳያቸው፡፡ እነርሱም በሰይፍ ስለት ከተማውን ወጉ፣ ያንን ሰውና ቤተሰቦቹንም እንዲያመልጡ አደረጓቻው፡፡ 26 ሰውየውም ወደ ኬጢያውያን ሐገር ሄደና ከተማ ገነባ ስሙንም ሎዛ አለው፣ የዚያ ቦታ ስምም እስከዛሬ ሎዛ ነው፡፡ 27 የምናሴ ሰዎች በቤትሳንና በመንደሮቿ፣ በታዕናክና በመንደሮቿ፣ በዶርና በመንደሮቿ፣ በይብለዓምና በመንደሮቿ፣ በመጊዶና በመንደሮቿ ይኖሩ የነበሩትን ሰዎች አላስወጡአቸውም፣ ምክንቱም ከነዓናውያን በዚያ ለመቀመጥ ወስነው ስለነበር ነው፡፡ 28 እስራኤልም በበረታ ጊዜ፣ ከነዓናውያንን የጉልበት ስራ እየሰሩ እንዲያገለግሉአቸው አስገደዷቸው፣ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ አላስወጧቸውም፡፡ 29 ኤፍሬም በጌዝር ይኖሩ የነበሩትን ከነዓናውያን አላስወጣቸውም፣ ስለዚህ ከነዓናውያን በእነርሱ መካከል በጌዝር መኖር ቀጠሉ፡፡ 30 ዛብሎንም በቂድሮን የሚኖሩትን ሰዎች ወይም በነህሎል ይኖሩ የነበሩትንም ሰዎች አላስወጣቸውም፣ ስለዚህ ከነዓናውያን በእነርሱ መካከል መኖር ቀጠሉ፣ ነገር ግን ዛብሎን ከነዓናውያን የጉልበት ስራ እየሰሩ እንዲያገለግሉአቸው ያስገድዳቸው ነበር፡፡ 31 አሴር በዓኮ፣ በሲዶን፣ በአሕላብ፣ በአክዚብ፣ በሒልባን፣ በአፌቅ፣ በረአብም የሚኖሩትን ሰዎች አላስወጣቸውም፡፡ 32 ስለዚህ የአሴር ነገድ በምድሪቱ በሚኖሩት በከነዓናውያን መካከል ኖሩ፣ ምክንያቱም አላስወጧቸውም ነበር፡፡ 33 የንፍታሌም ነገድ በቤት ሳሚስና በቤት ዓናት ይኖሩ የነበሩትን ሰዎችን አላስወጧቸውም፡፡ ስለዚህ የንፍታሌም ነገድ በምድራቸው ይኖሩ በነበሩ በነዓናውያን ሰዎች መካከል አብረው ኖሩ፡፡ ይሁን እንጂ የቤት ሳሚስና የቤት ዓናት ነዋሪዎች ለንፍታሌም ሰዎች የጉልበት ስራ እንዲሰሩ ይገደዱ ነበር፡፡ 34 አሞራውያንም የዳን ነገድ በኮረብታማው አገር እንዲኖሩ አስገደዷቸው፣ ወደ ሜዳማ ስፍራ ወርደው እንዲኖሩ አልፈቀዱላቸውም ነበር፡፡ 35 ስለዚህ አሞራውያን በሔሬስ ተራራ፣ በኤሎን፣ በሸዓልቢምም ኖሩ፣ ነገር ግን የዮሴፍ ቤት ወታደራዊ ኃይል በእነርሱ ላይ በረቱባቸው፣ ከዚህ የተነሳ ከባድ የጉልበት ስራ እየሰሩ 36 የአሞራውያንም ድንበር በሴላ ካለው ከአቅረቢም ኮረብታ ጀምሮ እስከ ኮረብታማው አገር ድረስ ነው፡፡



Judges 1:1

አያያዥ መግለጫ

መጽሐፈ መሳፍንት የኢያሱን ታሪክ የሚቀጥል ሲሆን በተጨማሪም የአዲሱ ታሪክ ክፍል ጅማሬም ነው።

ያህዌ

ይህ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለሕዝቡ የገለጠው ስሙ ነው። ያህዌን እንዴት መተርጎም እንደሚኖርብህ ለመገንዘብ የትርጉም ቃል ገጽን ተመልከት።

ከነዓናውያንን ማን ይወጋልናል

“እኛ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ሳይሆን የእስራኤልን ሕዝብ ነው።

ይሁዳ ይወጋቸዋል

እዚህ ጋ “ይሁዳ” የሚወክለው የይሁዳ ነገድ የሆነውን ሕዝብ ነው። በመጀመሪያ እንዲወጉ እግዚአብሔር እነዚህን ሰዎች ያዛቸዋል። አ.ት፡ “የይሁዳ ሰዎች በመጀመሪያ መውጋት አለባቸው”

ተመልከቱ

“እዩ” ወይም “ስሙ” ወይም “የምነግራችሁን ልብ በሉ”

ይህቺን ምድር

ይህ ከነዓናውያን ይኖሩበት የነበረውን ምድር ያመለክታል። አ.ት፡ “የከነዓናውያን ምድር”

ወንድሞቻቸው

“እስራኤላውያን ባልንጀሮቻቸውን” ወይም “ዘመዶቻቸውን”

ከእኛ ጋር ውጡ

የይሁዳና የስምዖን ነገድ ሰዎች ከተቀሩት እስራኤላውያን ሕዝቦች ጋር በዮርዳኖስ ወንዝ ሸለቆ ሰፍረው ነበር። ለይሁዳ ተሰጥቶት የነበረው ምድር ከሸለቆው በላይ በኩል፣ በኮረብታው ላይ ነበር። አንዳንድ ቋንቋዎች፣ አብዛኛውን ጊዜ ሰዎቹ ወደ ላይ መውጣታቸውን ወይም መውረዳቸውን አያመለክቱም። አ.ት፡ “ከእኛ ጋር ኑ” ወይም “ከእኛ ጋር ሂዱ”

ወደ ተመደበልን - ወደ ተመደበላችሁ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ወደ መደበልን … እግዚአብሔር ወደ መደበላችሁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እኛም ከእናንተ ጋር እንሄዳለን

“እኛም ደግሞ ከእናንተ ጋር እንሄዳለን” ወይም “በተመሳሳይ እኛም ከእናንተ ጋር እንሄዳለን”

Judges 1:4

የይሁዳ ሰዎች ተዋጉ

በውስጠ ታዋቂ የስምዖን ሰዎችም ከይሁዳ ሰዎች ጋር ሆነው መዋጋታቸውን ያመለክታል።

አሥር ሺህ ገደሉ

“10,000 ያህሉን ገደሉ” ወይም “ብዙ ሕዝብ ገደሉ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ከእነርሱ

“የከነዓናውያንና የፌርዛውያን ወታደሮች” ወይም “ጠላቶች”

ቤዜቅ

በከነዓን ተራራዎች ላይ ያለ አካባቢ። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አዶኒቤዜቅ

ይህ ሰው የከነዓናውያንና የፌርዛውያን ሰራዊት አለቃ ነበር። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እርሱን ተዋጉት

እዚህ ጋ “እርሱን” የሚያመለክተው በመሠረቱ አዶኒቤዜቅንና ሰራዊቱን ነው። አ.ት፡ “እርሱንና ሰራዊቱን ተዋጓቸው”

Judges 1:6

አሳደዱት

“አባረሩት”

ሰባ ነገሥታት

“70 ነገሥታት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የእጅና የእግሮቻቸው አውራ ጣት የተቆረጠባቸው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የእኔ ሰዎች የእጆቻቸውንና የእግሮቻቸውን አውራ ጣቶች እንዲቆርጡ ያዘዝኳቸው” ወይም “የእጅና የእግሮቻቸውን አውራ ጣት የቆረጥናቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከጠረጴዛዬ ስር ምግባቸውን ይለቅሙ ነበር

እነዚህ ነገሥታት ፍርፋሪ እንዲለቅሙ መገደዳቸው አዶኒቤዜቅ እነዚህን ነገሥታት ምን ያህል እንዳዋረዳቸው ያሳያል። እዚህ ጋ ምግብ “መልቀም” ማለት እንደሚመገቡት ያመለክታል። አ.ት፡ “ከጠረጴዛዬ ስር ፍርፋሪ ይበሉ ነበር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 1:8

የኢየሩሳሌምን ከተማ እና …ወሰዷት

እዚህ ጋ “ከተማ” የሚወክለው ሕዝብን ነው። አ.ት፡ “በኢየሩሳሌም ይኖሩ የነበሩትን ሰዎች እና … አሸነፏቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወጓት

እዚህ ጋ “እርሷ” የሚያመለክተው ከተማን፣ ይኸውም የሚኖሩባትን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “የከተማይቱን ሰዎች ወጓቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በሰይፍ ስለት

“በሰይፋቸው ጫፍ”። እዚህ ጋ “ሰይፍ” የሚወክለው ወታደሮች በጦርነት ውስጥ የሚጠቀሙበትን ሰይፍና ሌሎች የጦር መሣሪያዎች ነው። አ.ት፡ “በሰይፎቻቸው” ወይም “በጦር መሣሪያዎቻቸው”

የይሁዳ ሰዎች ለመዋጋት ወረዱ

ከኢየሩሳሌም በሚጓዙበት ጊዜ “ወረዱ” የሚለውን ቃል መጠቀም የተለመደ ነበር። አ.ት፡ “የይሁዳ ሰዎች ለመዋጋት ሄዱ”

በኔጌብ ውስጥ

“በደቡባዊው የይሁዳ ምድረ በዳ”

የኮረብታ ግርጌ

ከተራራ በታች ያሉ ኮረብታዎች ወይም የተራራ ወገብ

የኬብሮን ስም ቀድሞ ቂርያት አርባቅ ነበር

ይህ ዳራዊ መረጃ ነው። ይህንን መጽሐፍ በመጀመሪያ ያነበቡ አንዳንድ ሰዎች ምናልባት ቂርያት አርባቅ የሚለውን ሰምተው ይሆናል፣ ነገር ግን እርሱኑ የኬብሮን ከተማ ብለው እንደሚጠሩት አያውቁም ነበር። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ሴሲን፣ አኪመንና ተላሚን

እነዚህ በኬብሮን የሚኖሩ የሦስቱ ከነዓናውያን አለቆች ስም ነው። እያንዳንዱ አለቃ ሰራዊቱን ይወክላል። አ.ት፡ “ሴሲን፣ አኪመን፣ ተላሚና ሰራዊታቸው” (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ እና ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 1:11

የዳቤር ስም ቀድሞ ቅርያት ሤፍር ነበር

ደራሲው ምናልባት ይህንን የጻፈው አንባቢዎቹ ከተማይቱን በዳቤር ስም ስለሚያውቋት ይሆናል። እስራኤላውያን በወጓት ጊዜ ግን ቅርያት ሤፍር በመባል ትታወቅ ነበር። አ.ት፡ “ቂርያትሤፍር ተብላ የምትጠራውን” (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ቀድሞ

“ባለፈው ዘመን” ወይም “በድሮ ጊዜ”

ቂርያት ሤፍርን የሚወጋና የሚወስዳት

እዚህ ጋ “ቂርያት ሤፍር” የሚወክለው ሕዝቡን ነው። አ.ት፡ “የቂርያት ሤፍርን ሕዝብ የሚወጋና የሚያሸንፍ ከተማቸውንም የሚወስድ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዓክሳ

ይህ የካሌብ ሴት ልጅ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የቄኔዝ ልጅ ጎቶንያል

እነዚህ የወንዶች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 1:14

አጥብቃ ነገረችው

“ዓክሳ ለጎቶንያል አጥብቃ ነገረችው”

መሬቱን ሰጥተኸኛልና እርሻውን ስጣት

ይህ የሚያሳየው በቁጥር 14 ላይ በጠየቀችው ጊዜ እርሻውን እንደሰጣት ነው። በቁጥር 15 ደግሞ ከእርሻው በተጨማሪ የምንጩን ውሃ ትጠይቀዋለች።

በረከትን ስጠኝ

“ውለታ ዋልልኝ” ወይም “ይህንን አድርግልኝ”

የኔጌብን ምድር ሰጥተኸኛልና

ካሌብ ዓክሳን ለጎቶንያል ስለዳረለት ጎቶንያል በማረካት በኔጌብ ከተማ ከእርሱ ጋር ኖረች። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉሙ መብራራት መቻል አለበት። አ.ት፡ “በኔጌብ እንድኖር እስከዳርከኝ ድረስ”

Judges 1:16

የሙሴ አማት

“የሙሴ የሚስቱ አባት”

ቄናዊው አማቱ ወጣ

“ከቄናውያን ሰዎች አንዱ የሆነው አማቱ ወጣ”

ከዘንባባዎቹ ከተማ ወደ ምድረበዳው ወጣ

“የዘንባባዎቹን ከተማ ትቶ … ወደ ምድረበዳ ወጣ”

የዘንባባዎች ከተማ

ይህ የኢያሪኮ ሌላኛው ስም ነው።

አራድ

ይህ በከነዓን የሚገኝ የአንድ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የወንድሞቻቸው የስምዖን ሰዎች

እዚህ ጋ “ወንድሞች” ማለት በሌላው የእስራኤል ነገድ ውስጥ የሚኖሩ ዘመዶች ማለት ነው።

ጻፋት

ይህ በከነዓን የሚገኝ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የከተማይቱ ስም ሔርማ ተብሎ ተጠራ

እስራኤላውያን ጻፋትን ከደመሰሷት በኋላ ስሟን ሔርማ ብለው ቀየሩት። “ሔርማ” ማለት “ፈጽሞ መጥፋት” ማለት ነው። (እና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 1:18

እግዚአብሔር ከይሁዳ ሕዝብ ጋር ነበር

እዚህ ላይ “ከ. . . ጋር” ማለት እግዚአሔር የይሁዳን ሕዝብ ረድቶታል ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሜዳ

ዛፍ የሌለበት፣ በጣም ሰፊ ለጥ ያለ መሬት

Judges 1:20

ኬብሮን ሙሴ እንዳለው ለካሌብ ተሰጥታ ነበር

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሙሴ ኬብሮንን ለካሌብ ሰጥቶት ነበር” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሦስቱን የዔናቅ ወንዶች ልጆች

የሕዝብ ወገን መሪዎች የሆኑት መላውን ማኅበር ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል። አ.ት፡ “የዔናቅ ሦስቱ ወንዶች ልጆቹና ሰዎቻቸው”

ዔናቅ

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። ዔናቅና ተወላጆቹ በረጅም ቁመታቸው የታወቁ ነበሩ። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እስከ ዛሬ ድረስ

“እስካሁን ድረስ”። ይህ የሚያመለክተው መጽሐፈ መሳፍንት የተጻፈበትን ጊዜ ነው።

Judges 1:22

የዮሴፍ ቤት

እዚህ ጋ “ቤት” የሚወክለው ተወላጆችን ነው። ምናሴና ኤፍሬም የዮሴፍ ልጆች ሲሆኑ የ “ዮሴፍ ቤት” የምናሴንና የኤፍሬምን ተወላጆች ሊያመለክት ይችላል። አ.ት፡ “የምናሴና የኤፍሬም ተወላጆች” ወይም “የምናሴና የኤፍሬም ነገድ ሰዎች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቤቴልን ለመውጋት

እዚህ ጋ “ቤቴል” የሚያመለክተው በቤቴል የሚኖሩትን ሰዎች ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰላይ

በምስጢር መረጃ ለማግኘት

ቀድሞ ሎዛ ተብላ ትጠራ የነበረችውን ከተማ

ይህ የዳራው መረጃ ነው። በመጀመሪያ ይህንን መጽሐፍ ያነበቡት ሰዎች ምናልባት ቤቴል ብለው የሚጠሯት ከተማ ሎዛ እንደነበረች አያውቁም ይሆናል። (ዳራዊ መረጃ እና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሰላዮች

በምስጢር መረጃ የሚያገኙ ሰዎች

Judges 1:25

ከተማይቱን ወጉ

እዚህ ጋ “ከተማ” የሚወክለው ሕዝቡን ነው። አ.ት፡ “የከተማይቱን ሰዎች ወጉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በሰይፍ ስለት

“በሰይፍ ጫፍ”። “ሰይፍ” እዚህ ጋ የሚወክለው ሰዎች በጦርነት ጊዜ የሚጠቀሙባቸውን ሰይፍና ሌሎች የጦር መሣሪያዎችን ነው። አ.ት፡ “በሰይፎቻቸው” ወይም “በጦር መሣሪያዎቻቸው”

ሂድ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አምልጥ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሎዛ

በቤቴል አቅራቢያ፣ በኬጢያውያን ምድር የምትገኘው፣ እንደ አዲስ የተቆረቆረችውና ሰውየው የተዋት ይህች ከተማ በሎዛ ስም ትጠራ ነበር።

ይህ እስከ ዛሬ ድረስ ስሟ ነው

“እስካሁን ስሟ ነው”። እዚህ ጋ “እስከ ዛሬ ድረስ” የሚያመለክተው መጽሐፈ መሳፍንት የተጻፈበትን ጊዜ ነው።

Judges 1:27

ቤትሳን፣ ታዕናክ፣ ዶር፣ ይብለዓም፣ መጊዶ

እነዚህ የከተሞች ስም ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከነዓናውያን በዚያች ምድር ለመኖር ወስነው ስለነበር

“መወሰን” በአንድ ነገር ቁርጠኛ አቋም መያዝ ነው። አ.ት፡ “ከነዓናውያን ያችን ምድር ላለመተው ቁርጠኛ አቋም ይዘው ስለነበር”

እስራኤል በበረታ ጊዜ

እዚህ ጋ “እስራኤል” የሚወክለው ሕዝቡን ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ሕዝብ በበረታ ጊዜ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከነዓናውያን በጉልበት ሥራ እንዲያገለግሏቸው አስገደዷቸው

“ከነዓናውያን ከባድ ሥራ እንዲሠሩላቸው አስገደዷቸው”

Judges 1:29

ኤፍሬም … አልቻሉም

እዚህ ጋ “ኤፍሬም” ማለት የኤፍሬም ነገድ ሰዎች ወይም ወታደር ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ጌዝር

በኤፍሬም አካባቢ ከሚገኙ ከተሞች የአንዱ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 1:30

ዛብሎን አላስወጣቸውም

እዚህ ጋ “ዛብሎን” የሚወክለው የዛብሎንን ነገድ ሰዎች ወይም ወታደሮችን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቂድሮን - ነሀሎል

እነዚህ በከነዓን ምድር የሚገኙ ከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዛብሎን ግን አስገደዳቸው

እዚህ ጋ “ዛብሎን” የሚወክለው የዛብሎንን ነገድ ሰዎች ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከባድ ሥራ

“አስቸጋሪ ሥራ”

Judges 1:31

አሴር አላስወጣቸውም

እዚህ ጋ “አሴር” የሚወክለው የአሴርን ነገድ ሰዎች ወይም ወታደሮች ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዓኮ … ሲዶን … አሕላብ፣ አክዚብ፣ ሒልባ፣ አፌቅ … ረአብ

እነዚህ በከነዓን ምድር የሚገኙ ከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 1:33

ቤት ሳሚስ - ቤት ዓናት

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የቤት ሳሚስና የቤት ዓናት ነዋሪዎች ለንፍታሌም የጉልበት ሥራ ለመሥራት ተገደዱ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የንፍታሌም ሰዎች የቤት ሳሚስንና የቤት ዓናትን ሰዎች እንደ ባሪያ እንዲሠሩላቸው አስገደዷቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 1:34

እንዲወርዱ አልፈቀዱላቸውም

“ከመውረድ አስቆሟቸው”

ሜዳ

ዛፍ የሌለበት በጣም ለጥ ያለ ሰፊ መሬት

የሔሬስ ተራራ

ይህ የኤሎን ከተማ የተሠራበት ረጅም ኮረብታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ኤሎን - ሸዓልቢም

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የዮሴፍ ቤት ወታደራዊ ኃይል ድል አደረጋቸው

“የዮሴፍ ተወላጅ የሆነው ነገድ ሕዝብ ብርቱ ሠራዊት ስለነበራቸው ድል ሊያደርጓቸው ችለዋል”

የዮሴፍ ቤት

እዚህ ጋ “ቤት” የሚወክለው ተወላጆችን ነው። ምናሴና ኤፍሬም የዮሴፍ ልጆች ሲሆኑ የ“ዮሴፍ ቤት” የምናሴንና የኤፍሬምን ተወላጆች ሊያመለክት ይችላል። አ.ት፡ “የምናሴና የኤፍሬም ተወላጆች” ወይም “የምናሴና የኤፍሬም ነገድ ሰዎች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የአቅረቢም ኮረብታ

ይህ ከሙት ባህር በደቡብ ምዕራብ በኩል የሚገኝ መተላለፊያ ነበር። “የጊንጥ መተላለፊያ” በመባልም ይጠራል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሴላዕ

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 2

1 የእግዚአብሔር መልዓክም ከጌልጌላ ወደ ቦኪም ወጣ፣ እንዲህም አለ፣ “ከግብጽ አወጣኋችሁ፣ ለአባቶቻችሁ ወደማልሁላቸው ምድር አመጣኋችሁ፡፡ እንዲህም አልሁ፣ ‘ከእናንተ ጋር ያለኝን ቃል ኪዳን አላፈርስም፡፡ 2 በዚህ ምድር ከሚኖሩ ሰዎች ጋር ቃል ኪዳን አትግቡ፡፡ መሰዊያቸውን ማፍረስ አለባችሁ፡፡’ እናንተ ግን ቃሌን አልሰማችሁም፡፡ ይህ ያደረጋችሁት ምንድን ነው? 3 አሁንም እላለሁ፣ ‘ከነዓናውያንን ከእናንተ ፊት አላወጣም፣ ነገር ግን እነርሱ የጎን እሾህ ይሆኑባችኋል፣ ጣዖቶቻቸውም ለእናንተ ወጥመድ ይሆናሉ፡፡’” 4 የእግዚአብሔር መልዓክም እነዚህን ቃሎች ለእስራኤል ሕዝብ ሁሉ በተናገረ ጊዜ ሕዝቡ ጮሁ አለቀሱም፡፡ 5 ያንንም ቦታ ቦኪም ብለው ጠሩት፡፡ በዚያም ለእግዚአብሔር መስዋዕትን አቀረቡ፡፡ 6 ኢያሱም ሰዎችን ወደ መንገዳቸው በላካቸው ጊዜ፣ የእስራኤል ሕዝብ ምድሩን ለመውሰድና የራሳቸው ለማድረግ ለእንዳንዳቸው ወደተመደበላቸው ቦታ ሄዱ፡፡ 7 ኢያሱ በሕይወት በነበረበት ዘመን፣ የእግዚአብሔርን ታላቅ ስራንና ለእስራኤል ምን እንዳደረገም ያዩ ከእርሱ በኋላም በኖሩ ሽማግሌዎች ዘመን ሁሉ ሕዝቡ እግዚአብሔርን አገለገለ፡፡ 8 የእግዚአብሔር አገልጋይ፣ የነዌ ልጅ ኢያሱ፣ በመቶ አስር ዓመቱ ሞተ፡፡ 9 እነርሱም በኤፍሬም ኮረብታማው አገር በሰሜናዊው ገአስ ተራራ በምድሪቱ ድንበር በተዘጋጀለት ቦታ በተምናሔሬስ ቀበሩት፡፡ 10 ያ ሁሉ ትውልድም ወደ አባቶቻቸው ተሰበሰቡ፡፡ ከእነርሱም በኃላ እግዚአብሔርንና እርሱ ለእስራኤል ያደረገውን ነገር የማያውቅ ሌላ ትውልድ ተነሳ፡፡ 11 የእስራኤል ሕዝብም በእግዚአብሔር ዓይን ክፉ የሆነውን ነገር አደረጉ፣ የበኣል አማልክትንም አመለኩ፡፡ 12 ከግብጽ ምድር ያወጣቸውን የአባቶቻቸውን አምላክ እግዚአብሔርን ተዉ፡፡ ሌሎች አማልክትን፣ በዙርያቸው የነበሩ ሕዝቦች አማልክትን ተከተሉ፣ ለእነርሱም ሰገዱ፡፡ እግዚአብሔርንም አስቆጡት ምከንያቱም 13 እግዚአብሔርን ትተዋልና፣ በኣልንና አስታሮትንም አምልከዋልና፡፡ 14 የእግዚአብሔርም ቁጣ በእስራኤል ላይ ነደደ፣ ንብረታቸውን ለሰረቋቸው ወራሪዎች አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ራሳቸውን ከጠላታቸው መከላከል እንዳይችሉ፣ በዙርያቸው በጠላቶቻቸው ብርታት ተይዘው እንደ ነበሩት ባርያዎች አሳልፎ ሸጣቸው፡፡ 15 እስራኤል ለውጊያ በምትሄዱበት ስፍራ ሁሉ፣ ለእነርሱ እንደማለላቸው ይሸነፉ ዘንድ የእግዚአብሔር እጅ በእነርሱ ላይ ይከፋ ነበር፡፡ ከዚህ የተነሳ እነርሱም በጣም ተጨነቁ፡፡ 16 ያን ጊዜ ንብረታቸውን ከሚሰርቋቸው ሰዎች ኃይል ያድናቸው ዘንድ እግዚአብሔር መሳፍንትን አስነሳላቸው፡፡ 17 ይሁን እንጂ እነርሱ መሳፍንቶቻቸውን ሊሰሟቸው አልቻሉም፡፡ ለእግዚአብሔር አልታመኑም፣ ራሳቸውንም እንደ አመንዝራዎች ለሌሎች አማልክት ሰጡ፣ አመለኳቸውም፡፡ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ይከተሉ ከነበሩት ከአባቶቻቸው መንገድ ወዲያውኑ ዘወር አሉ፣ እነርሱ ራሳቸው እንደ አባቶቻቸው አላደረጉም፡፡ 18 እግዚአብሔር ለእነርሱ መሳፍንትን ባስነሳላቸው ጊዜ፣ መሳፍንቱ በኖሩበት ዘመን ሁሉ እግዚአብሔር መሳፍንቱን ረዳቸው፣ ከጠላቶቻቸውም ጉልበት ሁሉ አዳናቸው፡፡ በጨቆኗቸውና መከራ ባሳዩአቸው ሰዎች ምክንያት ወደ እርሱ በጮኹ ጊዜ እግዚአብሔር ለእነርሱ አዘነላቸው፡፡ 19 ነገር ግን መስፍኑ በሞተ ጊዜ፣ ተመልሰው አባቶቻው ያደርጉ ከነበረውም እጅግ የከፋ ነገር አደረጉ፡፡ ሌሎች አማልክትን በመከተል እነርሱን ያገለግሉና ያመልኩ ነበር፡፡ ክፉ ድርጊታቸውንና እልኸኛ መንገዳቸውንም ለመተው ፈቃደኛ አልነበሩም፡፡ 20 የእግዚአብሔርም ቁጣ በእስራኤል ላይ ነደደ፣ እንዲህም አለ፣ “ይህ ሕዝብ ለአባቶቻቸው የገባሁትን ቃል ኪዳኔን ስላፈረሱ፣ ድምጼንም ስላልሰሙ 21 ከአሁን በኋላ ኢያሱ ሲሞት ሳያወጣቸው የተዋቸውን አሕዛብ ከፊታቸው አላወጣቸውም፡፡ 22 ይህን የማደርገው እስራኤል አባቶቻቸው እንዳደረጉት የእግዚአብሔርን መንገድ ይጠብቁና በዚያም ይሄዱ እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ እፈትናቸው ዘንድ ነው፡፡” 23 እግዚአብሔርም እነዚያን አሕዛብ የተዋቸው፣ በፍጥነትም ያላስወጣቸው፣ ኢያሱም እንዲያሸንፋቸው ያልፈቀደለት ለዚህ ነው፡፡



Judges 2:1

የእግዚአብሔር መልአክ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) “እግዚአብሔርን የሚወክል መልአክ” ወይም 2) “እግዚአብሔርን የሚያገለግል መልዕከተኛ” ወይም 3) መልአክ መስሎ ከሰው ጋር የተነጋገረውን እግዚአብሔርን ራሱን ያመለክት ይሆናል የሚሉት ናቸው።

ከጌልገላ ወደ ቦኪም ወጣ

“ጌልገላን ትቶ ወደ ቦኪም ሄደ”

ቦኪም

መልአኩ ሕዝቡን ከገሰጻቸው በኋላ እስራኤላውያን ለዚህ ስፍራ በ2፡5 ላይ የሰጡት ስም ይህ ነው። “ቦኪም” ማለት “ማልቀስ” ማለት ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አላቸው

የእግዚአብሔር መልአክ ለእስራኤል ሕዝብ መናገሩ ግልጽ ነው።

ከግብፅ አወጣችሁ

“ከግብፅ መራችሁ”

አባቶቻችሁ

“ቅድም አያቶቻችሁ” ወይም “የቀድሞ አባቶቻችሁ”

ከእናንተ ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳኔን አፈረሱ

ይህ ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “አደርግላችኋለሁ ያልሁትን እንዳላደርግ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ድምፄን አልሰማችሁም

“ድምፅ” እዚህ ጋ የሚወክለው እግዚአብሔር የተናገረውን ነው። አ.ት፡ “ትዕዛዞቼን አልጠበቃችሁም” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ይህ ያደረጋችሁት ምንድነው?

ይህ ጥያቄ የተጠየቀው የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሔርን እንዳልታዘዙና በዚህም ምክንያት መከራ እንደሚደርስባቸው እንዲገነዘቡ ነው። አ.ት፡ “የከፋ ነገር አድርጋችኋል” (መልስ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

Judges 2:3

አሁን እናገራለሁ፣ ‘…ወጥመድ አልሆንባችሁም’

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ ነው። ይህ ቀጥታ የሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ተቆጥሮ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “…ወጥመድ እንደማልሆንባችሁ አሁን እነግራችኋለሁ”

ለጎናችሁ እሾህ ይሆናሉ

ከነዓናውያን እስራኤላውያንን ማስቸገራቸው ለእስራኤላውያን የጎን ውጋት እንደሚሆኑባቸው ተነግሯል። አ.ት፡ “መከራ ያመጡባችኋል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እሾኽ

እስከ 7 ሴንቲ ሜትር የሚረዝምና ከአንዳንድ እጽዋት ጋር አብሮ የሚበቅል ትናንሽ የሚወጉ ነገሮች ያሉበት እንጨት

አማልክቶቻቸው ወጥመድ ይሆኑባችኋል

እስራኤላውያኑ የከነዓናውያንን አማልክት ማምለካቸው ልክ አደን የሚያድን ሰው ያጠመደው ወጥመድ እንስሳውን ይዞ ለሞት እንደሚዳርገው ሁሉ ሐሰተኞቹ አማልክት አጥፊዎቻቸው እንደሚሆኑ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ጮኹና አለቀሱ

“በብዙ ዕንባ አለቀሱ”

Judges 2:6

አሁን ኢያሱ በ … ጊዜ

እዚህ ጋ “አሁን” የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው ዋነኛው ታሪክ የተገታበትን ለመለየት ነው። እዚህ ላይ ከኢያሱ በኋላ የነበረው ትውልድ እንዴት ኃጢአትን እንደ ሠሩና ሐሰተኞች አማልክትን እንዳመለኩ፣ እግዚአብሔር እንደቀጣቸው ሆኖም እንዲታደጓቸው መሳፍንትን እንደላከላቸው ተራኪው ጠቅለል ያለ ማብራሪያ መስጠት ይጀምራል። ይህ ማጠቃለያ የሚያበቃው በ2፡23 ላይ ነው።

ኢያሱ 110 ዓመት ሆኖት በሞተ ጊዜ

በ1፡1-2፡5 ላይ ያለው ሁነት የተፈጸመው ከኢያሱ ሞት በኋላ ነው። ይህ በኢያሱ መጽሐፍ መጨረሻ የተፈጸሙት ሁነቶች በድጋሚ የታሰቡበት ነው።

ወደ ተመደበላቸው ስፍራ

ይህ አገላለጽ በይበልጥ ግልጽ መሆን ይችላል። አ.ት፡ “ እግዚአብሔር ወደ ሰጣቸው ስፍራ”

በሕይወት ዘመኑ

ይህ ማለት አንድ ሰው የኖረበት ጊዜ ማለት ነው። አ.ት፡ “ዕድሜውን ሙሉ”

ሽማግሌዎች

ይህ ማለት የሙሴን ሕግ ከማስጠበቅ አንጻር በማኅበራዊ ፍትሕና ሀይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ እስራኤላውያንን ሲረዱ የነበሩ ሰዎች ናቸው።

ከእርሱ የበለጠ ኖረዋል

ይህ ማለት ከሌላው የበለጠ ዓመት መኖር ነው። አ.ት፡ “እርሱ ከኖረው የበለጠ ኖረዋል”

ነዌ

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

110 ዓመት ዕድሜው ላይ

“አንድ መቶ አሥር ዓመት ዕድሜው ላይ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 2:9

ወደ ተመደበለት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ወደ ሰጠው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ተምና ሔሬስ

ይህ በምድሪቱ ላይ የአንድ አካባቢ ስም ነው።

ገዓስ ተራራ

ይህ የአንድ ተራራ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ያ ትውልድ ሁሉ ደግሞ ወደ አባቶቻቸው ተሰብስበው ነበር

“ደግሞም ወደ አባቶቻቸው ተሰብስበው ነበር” የሚለው ሐረግ የዚያ ትውልድ ሰዎች ሲሞቱ ከእነርሱ በፊት የሞቱት አባቶቻቸው ወዳሉበት ወደዚያው ስፍራ ነፍሶቻቸው ሄዷል ማለት ነው። መሞታቸውን በትህትና የመግለጽ መንገድ ነው።

አባቶች

ይህ ማለት የአንድ ሰው ወይም የአንድ ሕዝብ ወገን የሆኑ አያቶች ማለት ነው።

አረጀ

“ዕድሜው ገፋ” ወይም “ሸመገለ”

እግዚአብሔርን የማያውቅ

እዚህ ጋ “የማያውቅ” ማለት የቀደመው ትውልድ ያውቅ እንደ ነበረ እግዚአብሔር ወይም የእርሱ ኃይል በሕይወታቸው የሚሠራውን ያልተለማመዱ ማለት ነው።

Judges 2:11

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የሚወክለው ፍርዱን ወይም ምዘናውን ነው። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ፍርድ ክፉ የሆነውን” ወይም “እግዚአብሔር ክፉ ነው ያለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የበኣል አማልክትን

ይህ የበኣል ብዙ ቁጥር ነው። “በኣል” የአንድ ሐሰተኛ አምላክ ስም ሆኖ ሳለ ቃሉ አብዛኛውን ጊዜ ከበኣል ጋር ለሚመለኩ ለሌሎች የተለያየዩ አማልክትም ጥቅም ላይ ውሏል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከእግዚአብሔር ተለዩ

ከእንግዲህ እግዚአብሔርን የማይታዘዙ እስራኤላውያን፣ በአካል ከእርሱ እንደተነጠሉና እንደተዉት ተቆጥሮ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አባቶቻቸው

“አያቶቻቸው” ወይም “የቀደሙት አባቶቻቸው”

ሌሎች አማልክትን ተከተሉ

የእስራኤላውያኑ ሐሰተኞች አማልክትን ማምለክ መጀመር እስራኤላውያን ሐሰተኞች አማልክትን ተከትለው እንደሄዱ ተቆጥሮ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰገዱላቸው

ይህ የአምልኮትና ለአንድ ሰው አክብሮትን የመስጠት ተግባር ነው።

እግዚአብሔርን ለቁጣ አነሣሡት

“እግዚአብሔር እንዲቆጣ አስደረጉት”

አስታሮቶች

ይህ የአስታሮት ብዙ ቁጥር ሲሆን በተለያዩ ቅርጾች የምትመለክ እንስት አምላክ ናት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 2:14

የእግዚአብሔር ቁጣ በእስራኤል ላይ ነደደ

የእግዚአብሔር ቁጣ እንደ እሳት እንደሚቃጠል ተገልጿል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በእስራኤል ሕዝብ ላይ በጣም ተቆጣ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሀብታቸውን ለሚቀሟቸው ለወራሪዎች አሳልፎ ሰጣቸው

“ወራሪዎች ሀብታቸውን እንዲቀሟቸው ተዋቸው”

ከእንግዲህ ራሳቸውን ከጠላቶቻቸው መከላከል እንዳይችሉ፣ በዙሪያቸው ለተገዙላቸው ጠላቶቻቸው እንደ ባሪያ ሸጣቸው።

ጠላቶች እስራኤላውያኑን እንደ ባሪያ አድርገው እንዲወስዷቸው እግዚአብሔር መፍቀዱ ለባርነት ሸጣቸው ተብሎ ተነግሯል። “ለተገዙላቸው” የሚለው ቃል በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እርሱ፣ ጠላቶቻቸው ድል እንዲያደርጓቸውና ባሪያ አድርገው እንዲወስዷቸው፣ ከእንግዲህም ብርቱዎቹን ጠላቶቻቸውን መቋቋም እንዳይችሉ ፈቀደ”። (ዘይቤአዊ አነጋገር፣ አድራጊና ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ይሸነፉ ዘንድ የእግዚአብሔር እጅ በእነርሱ ላይ ነበረች

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው የእግዚአብሔርን እጅ ነው። አ.ት፡ “ያሸንፏቸው ዘንድ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸውን ረዳቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እጅግ ተጨንቀው ነበር

“እጅግ ተሠቃይተው ነበር”

ከዚያም እግዚአብሔር መሳፍንትን አስነሣላቸው

እግዚአብሔር እንዲፈርዱ ሰዎችን መሾሙ ሰዎችን እንዳነሣቸው ወይም ብድግ እንዳደረጋቸው ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእነዚያ እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚያመለክተው ኃይልን ነው። አ.ት፡ “ከጠላቶቻቸው ኃይል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መሳፍንታቸውን አልሰሙም

“መሳፍንታቸውን አልታዘዙም”

ራሳቸውን እንደ ሴተኛ አዳሪዎች ለሌሎች አማልክት ሰጡ፣ አመለኳቸውም

የሕዝቡ እግዚአብሔርን ከድቶ ሌሎች አማልክትን ማምለክ እንደ ሴተኛ አዳሪ እንዲቆጠሩ ማስደረጉ ተነግሯል። አ.ት፡ “ሐሰተኛ አማልክትን በማምለክ ከዱት”

አባቶቻቸው ከኖሩበት መንገድ ፈጥነው ተመለሱ

ሕዝቡ እግዚአብሔርን እንዳመለኩ እንደ ቀድሞ አባቶቻቸው ያለማድረጋቸው፣ ከአባቶቻቸው መንገድ ተመልሰው በሌላ አቅጣጫ እንደሄዱ እንዲነገርላቸው ሆኗል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አባቶቻቸው

“ቅድመ አያቶቻቸው” ወይም “የቀድሞ አባቶቻቸው”

Judges 2:18

እግዚአብሔር መሳፍንትን ባስነሣላቸው ጊዜ

እግዚአብሔር እንዲፈርዱ ሰዎችን መሾሙ ሰዎችን እንዳነሣቸው ወይም ብድግ እንዳደረጋቸው ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መሳፍንትን ለእነርሱ … አዳኑአቸው

“እነርሱ” የሚለው ቃል እስራኤላውያንን ያመለክታል።

የጠላቶቻቸው እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” እስራኤልን የሚጎዱበትን የጠላትን ኃይል ያመለክታል። አ.ት፡ “የጠላቶቻቸውን ኃይል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መስፍኑ በኖረበት ዘመን ሁሉ

“መስፍኑ በሕይወት እስከ ኖረ ድረስ”

ማዘን

ለአንድ ሰው ወይም ለአንድ ነገር የርኅራኄ መኖር

በጮኹ ጊዜ

አንድ ሰው ከመከራው የተነሣ የሚጮኸው ጩኸት፣ እስራኤላውያኑ በመከራቸው ጊዜ ስቃያቸውን ለመግለጽ ጥቅም ላይ ውሏል። አ.ት፡ “በተሠቃዩ ጊዜ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ተመለሱ

ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ከቶ ያለመታዘዛቸው በአካል ከእግዚአብሔር እንደ ተለዩ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አባቶቻቸው

“ቅድመ አያቶቻቸው” ወይም “የቀድሞ አባቶቻቸው”

ሄደው ሌሎች አማልክቶችን አገለገሉ፣ አመለኳቸውም

የእስራኤላውያን ሌሎች አማልክትን ማምለክ ከሌሎች አማልክት ኋላ እየተራመዱ እንደሄዱ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ሌሎች አማልክትን አገለገሉ፣ ሰገዱላቸውም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የትኛውንም ክፉ ሥራቸውን ወይም የእልኸኝነት መንገድ ለመተው እምቢ አሉ

“ክፉ ነገር ማድረጋቸውንና እልኸኛ መሆናቸውን ለማቆም እምቢ አሉ”። ይህ በአዎንታዊ አገላለጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ክፉ ነገር ማድረጋቸውንና እልኸኝነታቸውን ቀጠሉ”

Judges 2:20

የእግዚአብሔር ቁጣ በእስራኤል ላይ ነደደ

የእግዚአብሔር ቁጣ እንደ እሳት እንደ ነደደ ተገልጿል። ይህንን በመሳፍንት 2፡14 ላይ እንዴት እንደ ተረጎምከው ተመልከት።

ይህ ሕዝብ ተላልፏል

እዚህ ጋ “ሕዝብ” የሚወክለው ሰዎቹን ነው። አ.ት፡ “እነዚህ ሰዎች ተላልፈዋል” ወይም “እስራኤላውያኑ ተላልፈዋል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አባቶች

እዚህ ጋ፣ ይህ የሚያመለክተው የአንድ ሰው ወይም የአንድ ሕዝብ ወገን የሆኑ አያቶችን ነው።

እነርሱ ድምፄን አልሰሙም

እዚህ ጋ “ድምፅ” የሚወክለው እግዚአብሔር የተናገረውን ነው። አ.ት፡ “እኔ ያዘዝኳቸውን አልታዘዙም” ወይም “አልታዘዙኝም”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የትኞቹም ሕዝቦች

እዚህ ጋ “ሕዝቦች” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ከእስራኤል በፊት በከነዓን ይኖሩ የነበሩትን የሕዝብ ወገን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እነርሱ የእግዚአብሔርን መንገድ ይጠብቃሉ፣ ይሄዱበታልም

ሰዎች እንዲኖሩት ወይም እንዲያደርጉት እግዚአብሔር የሚፈልገው ሕይወት እንደ መንገድ ወይም ጎዳና ተደርጎ ተነግሯል። እግዚአብሔርን የሚታዘዝ ሰው በመንገዱ ላይ እየሄደ እንዳለ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ፈጥኖ አስወጥቶ በኢያሱ እጅ አልሰጣቸውም

እነዚህ ሁለት ሐረጎች የሚሉት አንድ ነገር ስለሆነ መጣመር ይችላሉ። አ.ት፡ “ኢያሱ ፈጥኖ እንዲያሸንፋቸውና እንዲያስወጣቸው አላደረገም”

በኢያሱ እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” ኃይልን የሚገልጽ ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን “ኢያሱ” ራሱንና ሰራዊቱን ይወክላል። አ.ት፡ “በኢያሱና በሰራዊቱ ኃይል ሥር” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የሚለውን ተመልከት)


Chapter 3

1 እግዚአብሔር እነዚህን ሕዝቦች ሳያስወጣ ያስቀራቸው እስራኤልን ይልቁንም ደግሞ በከነዓን በተደረጉት ጦርነቶች ያልተዋጉትን በእስራኤል የሚገኙትን እያንዳንዱ ሰው ይፈትን ዘንድ ነው፡፡ 2 (ይህንን ያደረገው ውጊያ የማያውቁትን አዲሱ የእስራኤል ትውልድ ውጊያን ለማስተማር ነው) ፡- 3 አምስቱ የፍልስጤማውያን ነገስታት፣ ከነዓናውያንም ሁሉ፣ ሲዶናውያን እና ከበዓልኤርሞንየም ተራራ እስከ ሐማት መግቢያ ድረስ በሊባኖስ ተራራዎች ይኖሩ የነበሩትም ኤውያውያን ነበሩ፡፡ 4 እነዚህ ሕዝቦች ሳይወጡ እንዲቀሩ የተደረጉት እግዚአብሔር እስራኤልን መፈተኛ እንዲሆኑ ነው፣ እነርሱ ለአባቶቻቸው በሙሴ በኩል የሰጣቸውን ሕግ ይታዘዙና አይታዘዙ እንደሆነ ለማረጋገጥ ነው፡፡ 5 ስለዚህ የእስራኤል ሕዝብ በከነዓናውያን፣ ከኬጢያውያን፣ ከአሞራውያን፣ ከፌርዛውያን ከኤውያውያንና ከኢያቡሳውያን ጋር አብረው ኖሩ፡፡ 6 ሴት ልጆቻቸውንም ሚስት እንዲሆኗቸው ወሰዷቸው፣ የራሳቸውን ሴት ልጆችም ለወንድ ልጆቻቸው ሰጧቸው፣ አማልክቶቻቸውንም አመለኩ፡፡ 7 የእስራኤል ሕዝብ በእግዚአብሔር ዓይን ጸያፍ የነበረውን ነገር ፈጸሙ፣ አምላካቸው እግዚአብሔርንም ረሱ፡፡ የኣልንና የአስታሮትን አማልክት አመለኩ፡፡ 8 ስለዚህም የእግዚአብሔር ቁጣ በእስራኤል ላይ ነደደ፣ ለመስጶጣምያ ንጉስ ለኩሰርሰቴም እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ የእስራኤል ሕዝብም ኩሰርሰቴን ለስምንት አመታት አገለገሉ፡፡ 9 የእስራኤል ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር በጮሁ ጊዜ፣ እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ለመርዳት የሚመጣና ካሉበት ሁኔታም የሚያድናቸው ሰው አስነሳ፡- ይህም ሰው የካሌብ ታናሽ ወንድም የቄኔዝ ልጅ ጎቶንያል ነበር፡፡ 10 የእግዚአብሔር መንፈስም አበረታው፣ እስራኤላውያን ላይም ይፈርድ ነበር፣ ወደ ውጊያም ይወጣ ነበር፡፡ እግዚአብሔርም በመስጶጣምያ ንጉስ በኩሰርሰቴ ላይ ድልን ሰጠው፡፡ ኩሰርሰቴንም ያሸነፈው የጎቶንያል እጅ ነበር፡፡ 11 ምድሪም ለአርባ ዓመት ሰላም አገኘች፡፡ የቄኔዝ ልጅ ጎቶንያልም ሞተ፡፡ 12 የእስራኤልም ሕዝብ ክፉ ነገሮችን በማድረግ ደግመው እግዚአብሔርን ሳይታዘዙ ቀሩ፣ እርሱም ምን እንዳደረጉ ተመለከተ፡፡ ስለዚህ እስራኤል ክፉ ነገሮችን ስላደረጉና፣ እግዚአብሔርም ስላያቸው የሞኣብ ንጉስ ኤግሎም እስራኤልን ለመውጋት በመጣ ጊዜ እግዚአብሔር ብርታትን ሰጠው፡፡ 13 ኤግሎምም ከአሞንና ከአማሌቃውያን ጋር ተባበረ፣ እነርሱም ሄዱ እስራኤልንም አሸነፉ፣ ከዚያም የዘንባባ ከተማን ተቆጣጠሩ፡፡ 14 የእስራኤልም ሕዝብ የሞኣብን ንጉስ ኤግሎምን ለአስራ ስምንት አመታት አገለገሉ፡፡ 15 ነገር ግን የእስራኤል ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር በጮሁ ጊዜ፣ እግዚአብሔር የሚረዳቸውን ሰው አስነሳ፣ ይህም ግራኝ የነበረው ብንያማዊው የጌራን ልጅ ናኦድ ነው፡፡ የእስራኤልም ሕዝብ እርሱን ወደ ሞኣብ ንጉስ ወደ ኤግሎም የሚከፍሉትን ግብር አስይዘው ላኩት፡፡ 16 ናኦድ በሁለት በኩል የተሳለ ርዝመቱ አንድ ክንድ የሆነ ሰይፍን ሰራ፤ ከልብሱም በታች በቀኝ ጭኑ አሰረው፡፡ 17 ግብሩንም ለሞኣብ ንጉስ ለኤግሎም ሰጠው፡፡ (ኤግሎም በዚያን ጊዜ እጅግ ወፍራም ሰው ነበር፡፡) 18 ናኦድም የግብሩን ክፍያ ካቀረበ በኋላ፣ ግብሩን ተሸክመው ገብተው ከነበሩ ሰዎች ጋር ወጣ፡፡ 19 ይሁን እንጂ ናኦድ በጌልጌላ አጠገብ የተቀረጹ ምስሎች ተሰርተውበት ወደነበረው ስፍራ ሲደርስ ተመልሶ ሄደና እንዲህ አለ፡- “ንጉስ ሆይ፣ ለአንተ የሚስጥር መልዕክት አለኝ፡፡” ኤግሎምም እንዲህ አለ፡- “ጸጥታ!” ስለዚህም አገልጋዮቹ ሁሉ ክፍሉን ትተው ወጡ፡፡ 20 ናኦድም ወደ እርሱ መጣ፡፡ ንጉሱም ቀዝቃዛ በሆነው ሰገነት ላይ ብቻውን ተቀምጦ ነበር፡፡ናኦድም እንዲህ አለ፣ “ለአንተ ከእግዚአብሔር የመጣ መልዕክት አለኝ፡፡” ንጉሱም ከመቀመጫው ተነሳ፡፡ 21 ናኦድም ግራ እጁን ዘረጋና ሰይፉን ከቀኝ ጭኑ አወጣ፣ ሰይፉንም በንጉሱ ሰውነት ውስጥ ሰካው፡፡ 22 የሰይፉም እጀታ ከስለቱ ጋር ወደ ሰውነቱ ገባ፣ ጫፉም በጀርባው ወጣ፣ ሞራም ስለቱን ሸፈነው፣ ናኦድም ሰይፉን ከንጉሱ ሰውነት አላወጣውም፡፡ 23 ከዚያም ናዖድ ወደ በረንዳው ወጣና የሰገነቱን በር በንጉሱ ላይ ዘግቶ ቈለፈው፡፡ 24 ናዖድም ከሄደ በኋላ፣ የንጉሱ ባሪያዎች መጡ፤ የሰገነቱም ደጅ ተቈልፎ አዩ፣ ስለዚህ እንዲህ ሲሉ አሰቡ፣ “ምናልባት በቀዝቃዛው ሰገነት ውስጥ እየተጸዳዳ ይሆናል፡፡” 25 ንጉሱ የሰገነቱን በር ሳይከፍት በቆየም ጊዜ ስራቸውን ችላ እንዳሉ እስኪሰማቸው ድረስ ስጋት እያደረባቸው ጠበቁ፡፡ ስለዚህ ቁልፉን ወሰዱና በሮቹን ከፈቱ፣ እነሆም ጌታቸው ተጋድሞ፣ በወለሉም ላይ ወድቆ፣ ሞቶም አገኙት፡፡ 26 ባርያዎቹ ምን ማድረግ እንዳለባቸው እያሰቡ ሲጠባበቁ፣ ናዖድ አመለጠ፣ የጣኦታት ምስል በተቀረጸበት ስፍራ በኩል አለፈ፣ ወደ ቤይሮታም አመለጠ፡፡ 27 በደረሰም ጊዜ፣ በኮረብታማው በኤፍሬም አገር ቀንደ መለከት ነፋ፡፡ ከዚያም የእስራኤል ሕዝብ ከእርሱ ጋር ከኮረብታማው አገር ወረዱ፣ እርሱም ይመራቸው ነበር፡፡ 28 እርሱም እንዲህ አላቸው፣ “ተከተሉኝ፣ እግዚአብሔር ጠላቶቻችሁን፣ ሞዓባውያንን በእጃችሁ አሳልፎ ሰጥቶአልና፡፡” እነርሱም ተከትለውት ወረዱና የዮርዳኖስን መሻገርያ ከሞዓባውያን ቀምተው ያዙ፣ እነርሱም ማንም ሰው ወንዙን እንዳይሻገር ከለከሉ፡፡ 29 በዚያን ጊዜም ከሞዓብ አሥር ሺህ የሚሆኑ ሰዎችን ገደሉ፣ የተገደሉትም ሁሉ ጠንካራና ኃይለኛ ሰዎች ነበሩ፡፡ አንድም እንኳ አላመለጠም፡፡ 30 በዚያም ቀን ሞዓብ በእስራኤል ብርታት ድል ሆነች፡፡ ምድሪቱም ለሰማንያ ዓመት ዐረፈች፡፡ 31 ከናኦድ በኋላ የተነሳው መስፍን ስድስት መቶ የፍልስጥኤም ሰዎችን በበሬ መንጃ የገደለው የዓናት ልጅ ሰሜጋር ነበር፡፡ እርሱም ደግሞ እስራኤልን ከአደጋ አዳነ፡፡



Judges 3:1

አሁን እግዚአብሔር

እዚህ ጋ “አሁን” የሚለው ቃል የታሪኩን አዲስ ክፍል ይጀምራል።

እነዚህ ሕዝቦች

ይህ ተራኪው በ3፡3 የሚዘረዝራቸውን የሕዝብ ወገኖች ያመለክታል።

በከነዓን በተደረጉት በየትኛውም ጦርነት ያልተሳተፉትን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በከነዓን በየትኛውም ጦርነት ያልተዋጉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ካሁን በፊት ጦርነት የማያውቁትን አዲሱን የእስራኤል ትውልድ ውጊያ ለማስተማር ይህንን አደረገ

ይህ ከዋናው የታሪክ መስመር ይነጠላል። እግዚአብሔር አንዳንድ የሕዝብ ወገኖችን ለምን በከነዓን እንዳስቀራቸው ተራኪው ዳራዊ መረጃ ይሰጣል። አ.ት፡ “ቀድሞ በጦርነት ያልተዋጉ ወጣቶችን እንዴት መዋጋት እንዳለባቸው ለማስተማር እግዚአብሔር በእስራኤላውያን መካከል ሕዝቦች እንዲቀሩ አደረገ” (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

አምስቱ ነገሥታት

እነዚህ አምስት ነገሥታት ራሳቸውንና ሕዝባቸውን ይወክላሉ። አ.ት፡ “አምስቱ ነገሥታትና ሕዝቦቻቸው”

በኣል አርሞንኤም ተራራ

ይህ በእስራኤል ረጅሙ ተራራ ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሐማትስ መተላለፊያ

ይህ በሰሜናዊ የከነዓን ወሰን የሚገኝ የቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 3:4

እነዚህ ሕዝቦች ቀሩ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እነዚህን ሕዝቦች በከነዓን አስቀራቸው” ወይም “እነዚህ ሕዝቦች በከነዓን መኖራቸውን እንዲቀጥሉ እግዚአብሔር ፈቀደላቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

እንደ ዘዴ

“እንደ መንገድ”

እንደሆን - ለአባቶቻቸው ሰጣቸው

“እነርሱ” እና “የእነርሱ” የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው።

እርሱ የሰጣቸውን ትዕዛዝ

“እግዚአብሔር የሰጣቸውን ትዕዛዝ”

Judges 3:7

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የሚወክለው የእግዚአብሔርን ፍርድ ወይም ምዘና ነው። ይህንን በመሳፍንት 2፡11 እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ፍርድ ክፉ የሆነውን” ወይም “እግዚአብሔር ክፉ ያለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አምላካቸውን እግዚአብሔርን ረሱ

እዚህ ጋ “ረሱ” ፈሊጣዊ አነጋገር ሲሆን ትርጉሙ “መታዘዛቸውን አቆሙ” የሚል ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የእግዚአብሔር ቁጣ ነደደ

የእግዚአብሔር በጣም መቆጣት በሚቀጣጠል እሳት ተመስሎ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በጣም ተቆጣ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በኩስርስቴም እጅ ሸጣቸው

የእስራኤል ሕዝብ እንዲሸነፍ መፍቀዱ እግዚአብሔር ለኩስርስቴም እንደ ሸጣቸው ተቆጥሮ ተነግሯል። አ.ት፡ “ኩስርስቴምና ሰራዊቱ ድል እንዲያደርጋቸው ፈቀደላቸው”

በኩስርስቴም እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” በፈሊጣዊ አነጋገር የሚወክለው ኃይልን ወይም መቆጣጠርን ነው። በተጨማሪም “ኩስርስቴም” ራሱንና ሰራዊቱን የሚወክል ተምሳሌት ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የሚለውን ተመልከት)

ኩስርስቴም

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አራም ነሃራይም

ይህ የአንድ ሀገር ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 3:9

እግዚአብሔር አንድ ሰው አስነሣ

እግዚአብሔር አንድ የተለየ ሥራ እንዲሠራለት አንዱን መሾሙ ከተቀመጠበት እንዳስነሣው ወይም ብድግ እንዳደረገው ተቆጥሮ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ጎቶንያል - ቄኔዝ

የእነዚህን ሰዎች ስም በመሳፍንት 1፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

ሾመው

ይህ ማለት ታላቅ መሪ ለመሆን የሚያስፈልገው ብቃት እንዲኖረውና እንዲያጎለብተው እግዚአብሔር ጎቶንያልን ረዳው ማለት ነው።

በእስራኤል ላይ ፈረደ

እዚህ ጋ “ፈረደ” ማለት የእስራኤልን ሕዝብ መራቸው ማለት ነው።

ወደ ጦርነት ሄደ

በዚህ አባባል ውስጥ “እርሱ” የሚያመለክተው ጎቶንያልን ራሱንና የእስራኤልን ሰራዊት ነው። አ.ት፡ “ጎቶንያልና የእስራኤል ወታደሮች ከኩስርስቴም ሰራዊት ጋር ለመዋጋት ሄዱ”

እግዚአብሔር በአራም ንጉሥ በኩስርስቴም ላይ ድልን ሰጠው

እዚህ ጋ “ኩስርስቴም” የራሱን ሰራዊት ይወክላል። አ.ት፡ “የእስራኤል ሰራዊት የአራም ንጉሥ የኩስርስቴምን ሰራዊት ድል እንዲያደርግ እግዚአብሔር ረዳቸው”

የጎቶንያል እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” ሰራዊትን የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የጎቶንያል ሰራዊት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ምድሪቱ ሰላም አገኘች

“ምድሪቱ” ጥቅም ላይ የዋለው በምድሪቱ የሚኖሩትን ሰዎች ለማመልከት ነው። አ.ት፡ “ሕዝቡ በሰላም ኖሩ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አርባ ዓመት

“40 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 3:12

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የሚወክለው የእግዚአብሔርን ፍርድ ወይም ምዘና ነው። ይህንን በመሳፍንት 2፡11 እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ፍርድ ክፉ የሆነውን” ወይም “እግዚአብሔር ክፉ ያለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር ለሞዓብ ንጉሥ ለዔግሎን ብርታትን ሰጠው

የነገር ስም የሆነው “ብርታት” እንደ ቅጽል ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የሞዓብን ንጉሥ ዔግሎንን አበረታው” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

እስራኤላውያንን ድል እንዲያደርጋቸው ለሞዓብ ንጉሥ ለዔግሎን

እዚህ ጋ “የሞዓብ ንጉሥ ዔግሎን” የሚወክለው ራሱንና ሰራዊቱን ነው። አ.ት፡ “የእስራኤልን ሰራዊት በሚወጉበት ጊዜ ለሞዓብ ንጉሥ ለዔግሎንና ለወታደሮቹ”

ዔግሎን

ይህ የንጉሥ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የዘንባባ ከተማ

ይህ ሌላው የኢያሪኮ ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 1፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

አሥራ ስምንት ዓመት

“18 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 3:15

ወደ እግዚአብሔር ጮኹ

ይህ ማለት በሩቅ ወዳለ ወደሌላው መጣራት ወይም ከፍ ባለ ድምፅ መናገር ማለት ነው። ደግሞም አንድ ሰው፣ በተለይም እግዚአብሔር እንዲረዳ መጠየቅ ሊሆንም ይችላል።

አንድ ሰው አስነሣላቸው

እግዚአብሔር አንድ የተለየ ሥራ እንዲሠራለት አንዱን መሾሙ ሰውየውን ከተቀመጠበት እንዳስነሣው ወይም ብድግ እንዳደረገው ተቆጥሮ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ናዖድ = ጌራ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ግራኝ

ናዖድ በግራ እጁ በተሻለ ሁኔታ ሰይፍ መያዝ ይችል ነበር።

Judges 3:16

አንድ ክንድ

ዘመናዊ የርዝመት መለኪያ መጠቀም የሚያስፈልግ ከሆነ ይህንን ለማድረግ ሁለት መንገዶች አሉ። አ.ት፡ “46 ሴንቲ ሜትር” ወይም “ግማሽ ሜትር ገደማ” (ርቀት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚለውን ተመልከት)

በቀኝ ታፋው በኩል በልብሱ ውስጥ ታጠቀው

“በቀኝ መታጠቂያው በኩል በልብሱ ስር ታጠቀው”

ታፋ

በወገብና በጉልበት መካከል ያለ የእግር ክፍል

በዚህ ጊዜ ዔግሎን በጣም ወፍራም ሰው ነበር

እዚህ ጋ “በዚህ ጊዜ” ጥቅም ላይ የዋለው ዋናው የታሪኩ መስመር መቆሙን ምልክት ለማድረግ ነው። እዚህ ጋ ተራኪው ስለ ዔግሎን ዳራዊ መረጃ ይሰጣል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

Judges 3:19

የተቀረጹ ምስሎች ወደተሠሩበት ቦታ ወደ ጌልጌላ አቅራቢያ በደረሰ ጊዜ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሰዎች የተቀረጹ ምስሎች ወደ ሠሩበት ወደ ጌልጌላ አቅራቢያ በደረሰ ጊዜ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በነፋሻማው የላይኛው ክፍል

ይህ ከዝቅተኛው ቀጥሎ ወደ ላይ ያለ ክፍል ሲሆን ለማረፊያነትና በቀኑ ሞቃታማ ሰዓት ቀዝቀዝ ብሎአቸው የሚቆዩበት ክፍል ነው።

ንጉሡ ከመቀመጫው ተነሣ

መቆም፣ የእርሱን መልዕክት በማድመጥ እግዚአብሔርን የማክበር ምልክት ነው።

Judges 3:21

የሰይፉ ጫፍ በጀርባው በኩል ወጣ

“የሰይፉ ስለት መጨረሻ በጀርባው በኩል ወጣ”

በረንዳ

ጣሪያው የተሸፈነና ግድግዳው አጠር ያለ ውጫዊ ክፍል

Judges 3:24

በርግጥ ራሱን እያስታገሰ ነው

ይህ ስለሚጸዳዳ ሰው የሚነገር የትህትና አነጋገር ነው።

ተግባራቸውን ቸል ያሉ ያህል እስኪሰማቸው ድረስ

አንዳች ችግር ተፈጥሮ እንደሆነና የንጉሡን የግል ክፍሉን መክፈትም ቢሆን የእነርሱ ተግባር እንደሚሆን በማሰብ ሲጨነቁ ቆዩ።

ቁልፍ ወስደው ከፈቷቸው

“ቁልፍ ወስደው በሮቹን ከፈቷቸው”

Judges 3:26

አገልጋዮቹ ሲጠባበቁት ሳሉ - ናዖድ አመለጠ

ይህ የሚነግረን አገልጋዮቹ የላይኛውን ክፍል በሮች በመክፈት ንጉሡ ሞቶ ሳያገኙት በፊት የሆነውን ነገር ነው። አ.ት፡ “አገልጋዮቹ ከላይኛው ክፍል ውጪ በመጠበቅ ላይ እያሉ … ናዖድ አመለጠ”

ሴርታይም

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በደረሰ ጊዜ

ይህ በይበልጥ ግልጽ መሆን ይችላል። አ.ት፡ “ወደ ሴርታይም በደረሰ ጊዜ”

Judges 3:28

እግዚአብሔር ጠላቶቻችሁን ድል ያደርጋቸዋል

እስራኤላውያን ጠላቶቻቸውን እንዲያሸንፉ እግዚአብሔር መርዳቱ እግዚአብሔር ከጠላቶቻቸው ጋር ተዋግቶ ድል እንደሚያደርግ ጦረኛ ተቆጥሮ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

መሻገሪያዎቹን ያዙ

“መሻገሪያዎቹን መቆጣጠር ቻሉ”

መሻገሪያዎች

ጥልቀት የሌለውና በቀላሉ ሊሻገሩት የሚቻል የወንዝ አካባቢ

ማንም እንዲሻገር አልፈቀዱም

“ማንም እንዳይሻገር ከለከሉ”

አሥር ሺህ ሰዎች

“10,000 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ብቁ የሆኑ ሰዎች

“የሚችሉ ሰዎች” ወይም “በሚገባ መዋጋት የሚችሉ ሰዎች”

ሞዓብ ለእስራኤል ጉልበት ተገዛ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የእስራኤል ወታደሮች ሞዓባውያንን ድል አደረጓቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የእስራኤል ጉልበት

እዚህ ጋ “ጉልበት” የሚወክለው የእስራኤልን ሰራዊት ነው።

ምድሪቱ ዐርፋ ነበር

እዚህ ጋ “ምድር” የሚወክለው ሕዝብን ነው። አ.ት፡ “እስራኤላውያን በሰላም ኖሩ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰማንያ ዓመት

“80 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 3:31

መስፍን

እስራኤላውያን ነገሥታት ሳይኖሯቸው በፊት፣ ወደ ተስፋይቱ ምድር ከገቡ በኋላ፣ በችግራቸው ጊዜ እንዲመሯቸው እግዚአብሔር መሳፍንትን ሾመላቸው። መሳፍንት አብዛኛውን ጊዜ እስራኤላውያንን ከጠላቶቻቸው ይታደጓቸው ነበር።

ሰሜጋር

የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዓናት

የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

600 ሰዎች

“ስድስት መቶ ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በሬዎችን ለመንዳት የሚያገለግል በትር

በበሬ የሚያርሱ ገበሬዎች በሬዎቹ ወደ ፊት እንዲሄዱላቸው ለመምታት ሹልነት ያለው በትር ይጠቀሙ ነበር። አ.ት፡ “በሬዎቹን ለመንዳት የሚጠቀሙበት በትር” ወይም “በሬዎችን መምሪያ በትር”

እርሱም ደግሞ እስራኤልን ከአደጋ አዳናቸው

“አደጋ” የሚለው ቃል የእስራኤልን ሕዝብ ለመጉዳት የሞከሩ ጠላቶቻቸውን ያመለክታል። አ.ት፡ “እርሱም ደግሞ የእስራኤልን ሕዝብ ከጠላቶቻቸው አዳናቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 4

1 ናዖድም ከሞተ በኋላ፣ የእስራኤል ሕዝብ ክፉ ነገሮችን በመስራት እንደገና እግዚአብሔርን አልታዘዙም፣ እርሱም ምን እንዳደረጉ ተመለከተ፡፡ 2 እግዚአብሔርም በሐጾር ሆኖ ይገዛ በነበረው፣ በከነዓን ንጉሥ በኢያቢስ እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ የሠራዊቱም አለቃ ሲሣራ ተብሎ ይጠራ ነበር፣ እርሱም የአሕዛብ በሆነችው በአሪሶት ኖረ፡፡ 3 የእስራኤልም ሕዝብ ለእርዳታ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፣ ምክንያቱም ሲሳራ ዘጠኝ መቶ የብረት ሰረገሎች ነበሩት፣ እርሱም የእስራኤልን ሕዝብ ለሀያ ዓመት በኃይል አስጨንቆ ገዛቸው፡፡ 4 በዚያ ጊዜ ነቢይቱ የለፊዶት ሚስት ዲቦራ፣ በእስራኤል ላይ ዋነኛ ፈራጅ ነበረች፡፡ 5 እርስዋም በኮረብታማው በኤፍሬም አገር በራማና በቤቴል መካከል ካለው የዲቦራ ዘንባባ ዛፍ ስር ትቀመጥ ነበር፣ የእስራኤልም ሕዝብ ለክርክራቸው መፍትሔ ለማግኘት ወደ እርስዋ ይመጡ ነበር፡፡ 6 እርስዋም በንፍታሌም ውስጥ ካለው ከቃዴስ የአቢኒኤምን ልጅ ባርቅን ጠራች፡፡ እንዲህም አለችው፣ “የእስራኤል አምላክ፣ እግዚአብሔር፣ እንዲህ ይልሃል፣ ‘ወደ ታቦር ተራራ ሂድ፣ ከንፍታሌምና ከዛብሎን አሥር ሺህ ሰዎች ከአንተ ጋር ውሰድ፡፡ 7 እኔ የኢያቢስን ሠራዊት አዛዥ ሲሣራን በቂሶን ወንዝ አቅራቢያ ከሰረገሎቹና ከሰራዊቱ ጋር እንዲያገኝህ አስወጣዋለሁ፣ እኔም በእርሱ ላይ ድልን እሰጥሃለሁ፡፡’” 8-9 ባርቅም እንዲህ አላት፣ “አንቺ ከእኔ ጋር ከሄድሽ እኔም እሄዳለሁ፣ ነገር ግን አንቺ ከእኔ ጋር ካልሄድሽ እኔም አልሄድም፡፡” እርስዋም እንዲህ አለች፣ “በእውነት ከአንተ ጋር እሄዳለሁ፡፡ ይሁን እንጂ፣ አንተ የምትሄድበት መንገድ ወደ ክብር አያደርስህም፣ ምክንያቱም እግዚአብሔር ሲሣራን በጥንካሬዋ ድል ታደርገው ዘንድ ለሴት አሳልፎ ይሰጣልና፡፡” ከዚያም ዲቦራ ተነሥታ ከባርቅ ጋር ወደ ቃዴስ ሄደች፡፡ 10 ባርቅም የዛብሎንና የንፍታሌም ሰዎች በአንድነት ወደ ቃዴስ እንዲመጡ ጠራቸው፡፡ አሥር ሺህም ሰዎች ተከተሉት፣ ዲቦራም ከእርሱ ጋር ሄደች፡፡ 11 ቄናዊው ሔቤርም ከቄናውያን ራሱን ለየ፣ እነርሱም የሙሴ አማት የኦባብ ልጆች ነበሩ፣ እርሱም በቃዴስ አጠገብ በጻዕናይም በነበረው በበሉጥ ዛፍ ጥግ ድንኳኑን ተከለ፡፡ 12 ለሲሳራም የአቢኔኤም ልጅ ባርቅ ወደ ታቦር ተራራ እንደወጣ በነገሩት ጊዜ፣ 13 ሲሣራም ሰረገሎቹን ሁሉ፣ ዘጠኝ መቶ የብረት ሰረገሎች፣ ከእርሱም ጋር የነበሩትን ወታደሮቹን ሁሉ፣ የአሕዛብ ከሆነችው ከአሪሶት ወደ ቂሶን ወንዝ ሰበሰባቸው፡፡ 14 ዲቦራም ባርቅን እንዲህ አለችው፣ “ሂድ! ዛሬ እግዚአብሔር በሲሣራ ላይ ድል እንድታደርግ በእጅህ አሳልፎ የሚሰጥበት ቀን ነውና፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ከፊትህ አልወጣምን?” ስለዚህ ባርቅ ከታቦር ተራራ አብረውት ከነበሩት አስር ሺህ ሰዎች ጋር ወረደ፡፡ 15 እግዚአብሔርም የሲሣራን ሰራዊት ግራ አጋባ፣ ሰረገሎቹንም ሁሉ፣ ሠራዊቱንም ሁሉ፣ የባርቅም ሰዎች የሲሳራን ሰዎች አጠቋቸው፣ ሲሳራም ከሰረገላው ወርዶ በእግሩ ሸሸ፡፡ 16 ባርቅ ግን ሰረገሎችንና ሠራዊቱን እስከ አሪሶት ድረስ አባረራቸው፣ የሲሣራም ሠራዊት ሁሉ በሰይፍ ስለት ተገደሉ፣ አንድ ሰው እንኳ አልቀረም፡፡ 17 ሲሳራ ግን በእግሩ ወደ ቄናዊው ሔቤር ሚስት፣ ወደ ኢያዔል ድንኳን ሸሸ፣ ምክንያቱም በሐሶር ንጉስ በኢያቢስና፣ በቄናዊው በሔቤር ቤት መካከል ሰላም ስለነበር ነው፡፡ 18 ኢያዔልም ሲሣራን ለመገናኘት ወጣች እንዲህም አለችው፣ “ግባ፣ ጌታዬ ሆይ፤ ወደ እኔ ግባ አትፍራም፡፡” እርሱም ወደ እርስዋ ወደ ድንኳንዋ ገባ፣ በብርድ ልብስም ሸፈነችው፡፡ 19 እርሱም እንዲህ አላት፣ “ጠምቶኛልና፣ እባክሽ የምጠጣው ጥቂት ውኃ ስጭኝ፡፡” እርስዋም ከቆዳ የተሰራ የወተቱን ማስቀመጫ ከፍታ የሚጠጣ ሰጠችው፣ ከዚያም እንደገና ሸፈነችው፡፡ 20 እርሱም አላት፣ “በድንኳኑ በር ላይ ቁሚ፡፡ ሰውም ቢመጣና ‘በዚህ ሰው አለን?’ ብሎ ቢጠይቅሽ ‘የለም’ በይ፡፡” 21 ከዚያም የሔቤር ሚስት ኢያዔል የድንኳን ካስማ ወሰደች በእጅዋም መዶሻ ያዘች በቀስታ ወደ እርሱ ሄደች፣ እርሱም በከባድ እንቅልፍ ላይ ነበር፣ እርስዋም ካስማውን በጆሮ ግንዱ ላይ ሰካችው፣ ካስማውም ሰውነቱን ወግቶ አለፈና ወደ መሬት ጠለቀ፡፡ እርሱም ሞተ፡፡ 22 ባርቅም ሲሣራን ሲያባርር፣ ኢያዔል ልታገኘው ወጣችና እንዲህ አለችው፣ “ና፣ የምትፈልገውንም ሰው አሳይሃለሁ፡፡” እርሱም ወደ ውስጥ ከእርስዋ ጋር ገባ፣ እነሆም በዚያ ሲሣራ ሞቶ ተጋድሞ ነበር፣ ካስማውም በጆሮ ግንዱ ውስጥ ተሰክቶ አገኘው፡፡” 23 ስለዚህ በዚያ ቀን እግዚአብሔር የከነዓንን ንገሥ ኢያቢስን በእስራኤል ሕዝብ ፊት አሸነፈው፡፡ 24 የእስራኤል ሕዝብ ጉልበት የከነዓን ንጉሥ ኢያቢስን እስከሚያጠፉ ድረስ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየበረታ መጣ፡፡



Judges 4:1

ናዖድ

የዚህን ሰው ስም በመሳፍንት 3፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የሚወክለው የእግዚአብሔርን ፍርድ ወይም ምዘና ነው። ይህንን በመሳፍንት 2፡11 እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ፍርድ ክፉ የሆነውን” ወይም “እግዚአብሔር ክፉ ያለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር በከነዓን ንጉሥ በኢያቢስ እጅ ሸጣቸው

እዚህ ጋ “እጅ” የሚያመለክተው በእስራኤል ላይ የበረታውን የኢያቢስን ኃይል ነው። እግዚአብሔር ለኢያቢስ ኃይል ለመስጠት መወሰኑ እርሱ ሕዝቡን ለኢያቢስ እንደሸጣቸው ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በከነዓን ንጉሥ በኢያቢስ ኃይል እንዲሸነፉ ፈቀደ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ኢያቢስ - ሲሣራ

እነዚህ የወንዶቹ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሐጾር = ሐሮሼትሐጎይም

እነዚህ የከተሞች ወይም የቦታ ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዘጠኝ መቶ የብረት ሠረገላዎች

“900 የብረት ሠረገላዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሃያ ዓመት

“20 ዓመት”

Judges 4:4

አሁን

ይህ ቃል ዋነኛውን የታሪክ መስመር ለማቆም ምልክት ሆኖ ጥቅም ላይ ውሏል። እዚህ ጋ ተራኪው ስለ ዲቦራ ዳራዊ መረጃ ይናገራል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ዲቦራ

ይህ የአንዲት ሴት ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ለፊዶት

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

መስፍን

እግዚአብሔር እስራኤላውያንን በመከራቸው ጊዜ የሚመሯቸው መሳፍንትን ሾመላቸው። አብዛኛውን ጊዜ መሳፍንቱ ከጠላቶቻቸው ያድኗቸው ነበር።

የዲቦራ ዘንባባ

ይህ ዛፍ በዲቦራ ስም ተጠርቷል።

Judges 4:6

ባራቅ - አቢኒኤም

እነዚህ የወንዶቹ ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የታቦር ተራራ

ይህ የአንድ ተራራ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አሥር ሺህ ሰዎች

“10,000 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አወጣዋለሁ

እዚህ ጋ “እኔ” የሚለው ቃል እግዚአብሔርን ያመለክታል።

ሲሣራን አወጣዋለሁ

እዚህ ጋ “ሲሣራ” ራሱንና ሰራዊቱን ይወክላል። አ.ት፡ “ሲሣራንና ሰራዊቱን አወጣለሁ”

ማውጣት

ሰዎች ከምቹ ስፍራቸው ወጥተው እንዲመጡ ማድረግ

ሲሣራ - ኢያቢስ

የእነዚህን ወንዶች ስም በመሳፍንት 4፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት

ቂሶን

ይህ የወንዝ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 4:8

ባርቅ

የዚህን ሰውዬ ስም በመሳፍንት 4፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

እየሄድክበት ያለው መንገድ ወደ ክብር አያደርስህም

ባርቅ የሚያደርገው ምርጫ የሚጓዝበትን መንገድ እንደ መምረጥ ተቆጥሯል። “ክብር”ም ለአንድ ተጓዥ እንደ መዳረሻ ተቆጥሮለታል። አ.ት፡ “በምታደርገው ነገር ማንም አያከብርህም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር ሲሣራን በሴት እጅ ላይ አሳልፎ ይሰጠዋል

እዚህ ጋ “እጅ” የሚያመለክተው እርሱን ለመግደል ያላትን ኃይል ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሲሣራን ሴት እንድታሸንፈው ያደርጋል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሲሣራ

የዚህን ሰውዬ ስም በመሳፍንት 4፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ዲቦራ

የዚህችን ሴት ስም በመሳፍንት 4፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Judges 4:11

አሁን

ይህ ቃል ዋነኛውን የታሪክ መስመር ለማቆም ምልክት ሆኖ ጥቅም ላይ ውሏል። እዚህ ጋ ተራኪው ስለ ቄናዊው ሔቤር ዳራዊ መረጃ ይናገራል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ሔቤር - ኦባብ

እነዚህ የወንዶች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ቄናዊ

ይህንን በመሳፍንት 1፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

የሙሴ አማች

“የሙሴ የሚስቱ አባት”

ጻዕናይም

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 4:12

ለሲሣራ በነገሩት ጊዜ

እዚህ ጋ “እነርሱ” የሚለው ቃል በተለየ ሁኔታ ማንንም አይገልጽም። አ.ት፡ “አንድ ሰው ለሲሣራ ሲነግረው”

ሲሣራ

የዚህን ሰውዬ ስም በመሳፍንት 4፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ባርቅ - አቢኒኤም - የታቦር ተራራ

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 4፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ሲሣራ ሠረገላዎቹን ሁሉ ሰበሰበ

እዚህ ጋ “ሠረገላዎች” የሚወክሉት ሠረገላዎቹን የሚነዱ ወታደሮችን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዘጠኝ መቶ የብረት ሠረገላዎች

“900 የብረት ሠረገላዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አሪሶት ሐጎይም

የዚህችን ከተማ ስም በመሳፍንት 4፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የቂሶን ወንዝ

ይህንን በመሳፍንት 4፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Judges 4:14

እግዚአብሔር ድልን ሰጥቶሃል

ዲቦራ ስለ ድሉ እርግጠኛ ስለ ነበረች ባርቅ አስቀድሞ ጦርነቱን እንዳሸነፈ አድርጋ ትናገራለች። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ድልን ይሰጥሃል”

የሚመራህ እግዚአብሔር አይደለምን?

የሚዋጉት ከእግዚአብሔር ጋር ወግነው መሆኑን ባርቅን ለማስታወስ ዲቦራ ይህንን ጥያቄ ትጠይቃለች። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እንደሚመራህ አስታውስ” (መልስ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ከአሥር ሺህ ጋር

“ከ10,000 ጋር” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 4:15

እግዚአብሔር ሲሣራን፣ ሠረገላዎቹንና ሰራዊቱን ሁሉ አደናገራቸው

“እግዚአብሔር፣ ሲሣራን፣ ሠረገላዎቹንና ሰራዊቱን ሁሉ በአግባቡ ማሰብ እንዳይችሉ አደረጋቸው” ወይም “እግዚአብሔር፣ ሲሣራ፣ ሠረገላዎቹና ሰራዊቱ ሁሉ እንዲደነግጡ አደረጋቸው”

ሠረገላዎቹ ሁሉ

እዚህ ጋ “ሠረገላዎቹ” የሚለው ቃል ሠረገላዎቹን የሚነዱትን ወታደሮች የሚያመለክት ፈሊጣዊ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ሠረገላዎቹን የሚነዱት ሰዎች ሁሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ባርቅ አሳደደ

እዚህ ጋ “ባርቅ” የሚወክለው ራሱንና ሰራዊቱን ነው። አ.ት፡ “ባርቅና ወታደሮቹ አሳደዱ”

አሪሶት

ይህንን በመሳፍንት 4፡2 ላይ በተረጎምክበት በዚያው መልክ ተርጉመው።

የሲሣራ ሰራዊት በሙሉ በሰይፍ ስለት ተገደሉ

እዚህ ጋ “ሰይፍ” የሚወክለው ወታደሮች በጦርነት ላይ የሚጠቀሙባቸውን ሰይፍና ሌሎች የጦር መሣሪያዎች ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ባርቅና ወታደሮቹ የሲሣራን ወታደሮች በሙሉ በሰይፍ ገደሏቸው”

Judges 4:17

ሲሣራ - ኢያቢስ - ሐጾር

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 4፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

በእግሩ ሸሸ

በፈረስ ወይም በሠረገላ ከመጋለብ ይልቅ በእግሩ መሮጡ ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ኢያዔል

ይህ የአንዲት ሴት ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሔቤር

የዚህን ሰውዬ ስም በመሳፍንት 4፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ቄናዊ

ይህንን በመሳፍንት 1፡16 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ዘወር በል

ይህ ማለት ከሚደረገው ጉዞ ለማረፍ የሚደረግ የመንገድ ለውጥ ነው። አ.ት፡ “ወዲህ ና”

ብርድ ልብስ

ከሱፍ ወይም ከእንስሳት ቆዳ የሚሠራና በመኝታ ጊዜ ሙቀት እንዲሰጥ የሚለበስ ሰፊ የአካል መሸፈኛ ነው።

Judges 4:19

ተናገራት

“ሲሣራ ለኢያኤል ተናገራት”

Judges 4:21

የድንኳን ካስማ

የድንኳኑን ማዕዘን ከምድር ጋር እንዲያያይዝ እንደ ትልቅ መንጠቆ በመዶሻ የሚመታ የሾለ እንጨት ወይም ብረት

መዶሻ

የድንኳኑን ካስማ ወደ መሬት ለማጥለቅ ክብደት ካለው እንጨት የሚሠራ መምቻ

ጥልቅ እንቅልፍ

አንድ ሰው ጥልቀት ካለው ጉድጓድ ውስጥ በቀላሉ መውጣት እንደማይችል ሁሉ ጥልቅ እንቅልፍ ውስጥ ያለ ሰውም በቀላሉ አይነቃም። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ባርቅ ያሳድደው ነበር

“ባርቅ ያባርረው ነበር” ወይም “ባርቅ ይከተለው ነበር”

Judges 4:23

እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ፊት የከነዓንን ንጉሥ ኢያቢስን ድል አደረገው

እግዚአብሔር እስራኤላውያኑ ኢያቢስንና ሰራዊቱን እንዲያሸንፏቸው ማድረጉ የእስራኤል ሕዝብ እያዩ እግዚአብሔር ራሱ ኢያቢስን ድል እንዳደረጋቸው ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ጉልበት

“ወታደራዊ ኃይል”

ደመሰሱት

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚያመለክተው ራሱንና ሰራዊቱን የሚወክለውን ኢያቢስን ነው። አ.ት፡ “ኢያቢስንና ሰራዊቱን ደመሰሱ”


Chapter 5

1 በዚያም ቀን ዲቦራና የአቢኒኤም ልጅ ባርቅ ይህንን መዝሙር ዘመሩ፡- 2 “በእስራኤል ውስጥ መሪዎች የመሪነት ስፍራውን ሲይዙ፣ ሕዝቡም በደስታና በፈቃዳቸው ለጦርነት ሲወጡ፣ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን! 3 ስሙ፣ እናንተ ነገሥታት! አድምጡ፣ እናንተም መኳንንት! እኔ፣ እኔ ለእግዚአብሔር እዘምራለሁ፤ ለእስራኤል አምላክ ለእግዚአብሔር ምስጋናን እዘምራለሁ፡፡ 4 እግዚአብሔር ሆይ፣ ከሴይር በወጣህ ጊዜ፣ ከኤዶምያስም በተነሳህ ጊዜ፣ ምድር ተናወጠች፣ ሰማያት ደግሞ ተንቀጠቀጡ፤ ደመናትም ደግሞ ውኃን አንጠባጠቡ፡፡ 5 ተራሮች በእግዚአብሔር ፊት ተንቀጠቀጡ፤ ሲና ተራራም እንኳ በእስራኤል አምላክ በእግዚአብሔር ፊት ተንቀጠቀጠ፡፡ 6 በዓናት ልጅ በሰሜጋር ዘመን፣ በኢያዔል ዘመን፣ መንገዶች ተተዉ፣ መንገደኞችም በጠመዝማዛ መንገድ ብቻ ይጠቀሙ ነበር፡፡ 7 እኔ ዲቦራ አለቃ እስከሆንሁበት ጊዜ ድረስ፣ ለእስራኤል እናት ሆኜ አለቅነትን እስከወሰድሁበት ጊዜ ድረስ፣ በእስራኤል ውስጥ ገበሬዎች አልነበሩም፡፡ 8 አዲስ አማልክትን መረጡ፣ በከተማዋ ደጆች ጦርነት ነበረ፤ በእስራኤል ውስጥ በአርባ ሺህ መካከል ጋሻ ወይም ጦር አልታየም፡፡ 9 ልቤ ወደ እስራኤል አለቆች ሄደ፣ በሕዝቡ መካከል ራሳቸውን በደስታ ስለ ሰጡትም እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፡፡ 10 እናንተ በነጫጭ አህዮች ላይ ትንሽ የምንጣፍ ኮርቻ ላይ ተቀምጣችሁ የምትጓዙ፣ በመንገድም የምትሄዱ እናንተ ስለዚህ ነገር አስቡ፡፡ 11 በማጠጫው ስፍራ መካከል ሆነው በጎችን የሚከፋፍሉትን ሰዎች ድምጽ ስሙ፡፡ የእግዚአብሔርን የጽድቅ ድርጊትና ተዋጊዎቹ በእስራኤል ውስጥ የሰሩትን የጽድቅ ተግባር በዚያ እንደገና እየተናገሩ ነው፡፡ ያን ጊዜ የእግዚአብሔር ሕዝብ ወደ ከተማው በሮች ወረዱ፡፡ 12 ንቂ፣ ንቂ፣ ዲቦራ ሆይ! ንቂ፣ ንቂ፣ መዝሙርን ዘምሪ! ባርቅ ሆይ፣ ተነሣ፣ የአቢኒኤም ልጅ ሆይ፣ ምርኮኞችህን ማርከህ ውሰድ፡፡ 13 የዚያን ጊዜ የተረፉት ወደ ኃያላኑ መጡ፣ ከተዋጊዎቹም መካከል የእግዚአብሔር ሕዝብ ወደ እኔ መጡ፡፡ 14 መሰረታቸው ከአማሌቅ ወገን የሆኑ ከኤፍሬም መጡ፤ የብንያም ሕዝብም ተከተሉህ፡፡ ከማኪርም አዛዦች ወረዱ፣ የስልጣን በትር የያዙ ከዛብሎን ወረዱ፡፡ 15 የይሳኮርም መሳፍንት ከዲቦራ ጋር ነበሩ፤ ይሳኮርም ከባርቅ ጋር በትዕዛዙ መሰረት ከኋላው እየተከተለ ወደ ሸለቆው ሄደ፡፡ በሮቤል ጎሳ መካከል ታላቅ የልብ ምርምር ነበረ፡፡ 16 የበጎች እረኞች ለመንጎቻቸው በፉጨት ሲጫወቱ እያዳመጥህ በእሳት ማንደጃ መካከል ለምን ተቀመጥህ? በሮቤል ጎሳ መካከል ታላቅ የልብ ምርምር ነበረ፡፡ 17 ገለዓድ በዮርዳኖስ ማዶ ተቀመጠ፤ ዳን ለምን በመርከብ ውስጥ ቀረ? አሴርም በባሕሩ ዳርቻ ቀረ፣ በወንዞቹም ዳርቻ ኖረ፡፡ 18 ዛብሎን ነፍሱን ወደ ሞት አሳልፎ የሚሰጥ ሕዝብ ነው፣ ንፍታሌምም በውጊያ ሜዳ ላይ ነው፡፡ 19 ነገሥታት መጡ ተዋጉም፣ የዚያን ጊዜ የከነዓን ነገስታትም በመጊዶ ውኆች አጠገብ በታዕናክ ተዋጉ፡፡ ምንም የብር ምርኮ አልወሰዱም፡፡ 20 ከሰማይ ከዋክብት ተዋጉ፣ በሰማያት ላይ በአካሄዳቸውም ሲሣራን ተዋጉት፡፡ 21 ከዱሮ ጀምሮ የታወቀው፣ የቂሶን ወንዝም፣ ጠርጎ ወሰዳቸው፡፡ ነፍሴ ሆይ ገስግሺ፣ በርቺ! 22 የፈረሶች የግልብያ ኮቴዎች ድምጽ፣ የኃያላኑ ግልቢያ ድምጽም፡፡ 23 የእግዚአብሔር መልአክ “ሜሮዝን እርገሙ!” ይላል፡፡ ‘ነዋሪዎቿን ፈጽማችሁ እርገሙ! ምክንያቱም እግዚአብሔርን ለመርዳት አልመጡም፣ ከኃያላን ጦረኞች ጋር በተደረገው ውጊያ እግዚአብሔርን ለመርዳት አልመጡምና፡፡' 24 የቄናዊው የሔቤር ሚስት፣ ኢያዔል፣ ከሴቶች ሁሉ ይልቅ የተባረከች ናት፣ በድንኳን ውስጥ ከሚኖሩ ሴቶች ሁሉ ይልቅ የተባረከች ናት፡፡ 25 ሰውየው ውኃ ለመናት፣ እርስዋም ወተት ሰጠችው፤ ለመሳፍንት በሚሆን በተከበረ ሳህን ቅቤ አመጣችለት፡፡ 26 እጅዋን ወደ ድንኳን ካስማ፣ ቀኝ እጅዋንም ወደ ሠራተኛ መዶሻ አደረገች፤ በመዶሻውም ሲሣራን መታች፣ ራሱንም ቀጠቀጠች፡፡ ጆሮ ግንዱን በወጋችው ጊዜ ጭንቅላቱንም ፈረከሰችው፡፡ 27 በእግሮችዋ መካከል ተደፋ፣ ወደቀ ተኛም፡፡ በእግሮችዋ አጠገብ ተሰብሮ ወደቀ፡፡ የተደፋበት ስፍራ በክፉ ሁኔታ የሞተበት ነው፡፡ 28 ከመስኮት ሆና ወደ ውጭ ተመለከተች፣ የሲሣራ እናት በርብራብ በኩል በኃዘን ወደ ውጭ ጮኸች፣ ‘ወደዚህ ለመምጣት ሰረገላው ረዥም ጊዜ ለምን ወሰደበት? ለምንስ ሰረገላዎቹን የሚጎትቱት የፈረሶቹ ኮቴዎች ዘገየ?’ 29 ብልሃተኞች ልዕልቶቿም መለሱላት፣ ለራስዋም ተመሳሳይ መልስ መለሰች፡- 30 ምርኮውን አግኝተው ተካፍለው የለምን? ለእያንዳንዱ ሰው ምርኮ አንዲት ወይም ሁለት ልጃገረድ፤ ለሲሣራ ምርኮ ልዩ ልዩ ቀለም ያለው ልብስ፣ የተጠለፈ ባለቀለም ጨርቅ ምርኮ፣ ለማረኩ ሰዎች ለአንገታቸው የሚሆን በሁለት እጥፍ የተጠለፈ ባለቀለም ጨርቆች ምርኮን አላገኙምን?’ 31 ስለዚህ፣ እግዚአብሔር ሆይ፣ ጠላቶችህ ሁሉ እንዲሁ ይጥፉ! ነገር ግን እርሱን የሚወዱት በኃይል እንደሚወጣ ጸሐይ ይሁኑ፡፡” ምድሪቱም ለአርባ ዓመት ያህል ዐረፈች፡፡



Judges 5:1

በዚያች ቀን

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በይበልጥ ግልጽ ሊደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እስራኤላውያን የንጉሥ ኢያቢስን ሰራዊት ድል ባደረጉበት ቀን”

ዲቦራ

ይህንን ስም በመሳፍንት 4፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ባርቅ - አቢኒኤም

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 4፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ሕዝቡ በፈቃዳቸው ራሳቸውን ለጦርነት በሰጡ ጊዜ

“ሰዎቹ ለመዋጋት በተስማሙ ጊዜ”

Judges 5:3

እናንተ ነገሥታት ስሙ! እናንት መሪዎች አድምጡ

ዲቦራና ባርቅ፣ ነገሥታትና መሪዎች እዚያ ተገኝተው መዝሙሩን ይሰሙ ይመስል ይናገራሉ።

እናንት ነገሥታቶች - እናንት መሪዎች

ይህ የሚያመለክተው በጥቅሉ ነገሥታትንና መሪዎችን እንጂ የተለዩ ነገሥታትን ወይም መሪዎችን አይደለም።

ከሴይር በወጣህ ጊዜ፣ ከኤዶም በተነሣህ ጊዜ

ይህ እስራኤላውያን በከነዓን የሚኖሩትን ድል ለማድረግ ኤዶምን ትተው የተነሡበትን ጊዜ ያመለክታል። እግዚአብሔር፣ ሕዝቡ የከነዓንን ሰዎች ድል እንዲያደርጓቸው ማብቃቱ እርሱ የእስራኤልን ሰራዊት እንደሚመራቸው ጦረኛ ተደርጎ እንዲነገርለት ሆኗል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሴይር

ሴይር በእስራኤልና በኤዶም ምድር ድንበር ላይ የሚገኝ ተራራ ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ምድር ተናወጠች፣ ሰማያትም ተንቀጠቀጡ፤ ደመናትም ደግሞ ውሃን አንጠባጠቡ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ይህ የምድር መናወጥንና ማዕበልን እንደሚፈጥር በመግለጽ ለእግዚአብሔር ኃይል አጽንዖት የሚሰጥ ሥነ ግጥማዊ ቋንቋ ነው ወይም 2) እስራኤላውያኑ በሚወጓቸው ጊዜ የከነዓን ሰዎች መፍራታቸው ሰማይና ምድር እንደተንቀጠቀጡ ተደርጎ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 5:5

ተራሮች ተንቀጠቀጡ

ይህ እግዚአብሔርን በጣም በመፍራታቸው ተራሮች መንቀጥቀጣቸውን ለማሳየት፣ ምናልባት የምድር መናወጥን ያመለክት ይሆናል። አ.ት፡ “ተራሮች በፍርሃት ተርበደበዱ”

በእግዚአብሔር ፊት

እዚህ ጋ “ፊት” የእግዚአብሔርን ሀልዎት ያመለክታል። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ሀልዎት ፊት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የሲና ተራራ እንኳን ተንቀጠቀጠ

ሙሴና እስራኤል በሲና ተራራ በነበሩ ጊዜ ተንቀጥቅጦ ነበር። አ.ት፡ “ከዓመታት በፊት የሲና ተራራ እንኳን ተንቀጥቅጧል”

በ… ቀናት

“በ… የሕይወት ዘመን”

ሰሜጋር = ዓናት = ኢያዔል

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው። ሰሜጋርና ዓናትን በመሳፍንት 3፡31 ላይ እንዲሁም ኢያዔልን በመሳፍንት 4፡18 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የዓናት ልጅ

ሰሜጋርንና የኖረበትን ዘመን መለየት እንዲቻል ለመርዳት የሰሜጋር አባት ተጠቅሷል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

አውራ ጎዳናዎቹ ተትተዋል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር የሚችል ሲሆን መንገዶቹ የተተዉበትን ምክንያት ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “የእስራኤልን ጠላቶች ስለ ፈሩ ሰዎች አውራ ጎዳናዎቹን መጠቀም አቆሙ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ፣ የሚለውን ተመልከት)

Judges 5:7

እኔ ዲቦራ እነሣለሁ = በእስራኤል እንደ እናት ሆነሽ ተነሽ

ዲቦራ ለትናንሽ ልጆች እንክብካቤ እንደምታደርግ እናት በእስራኤል ላይ መሪ ስለ መሆኗ ትናገራለች። አ.ት፡ “እኔ ዲቦራ መምራት ጀምሬአለሁ - እናት ልጆችዋን እንደምትንከባከብ እስራኤላውያንን እንከባከባለሁ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አዳዲስ አማልክትን መረጡ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ መቻል አለበት። አ.ት፡ “የእስራኤል ሕዝብ አዳዲስ አማልክትን አመለኩ”

በከተማይቱ በሮች ጦርነት ነበር

እዚህ ጋ “በሮች” መላውን ከተማውን ይወክላሉ። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉሙ በበለጠ ግልጽ መደረግ መቻል አለበት። አ.ት፡ “በእስራኤል ከተሞች ውስጥ ጠላት ሕዝቡን አጠቃ”

በእስራኤል በአርባ ሺዎቹ መካከል ጦር ወይም ጋሻ አልታየም

ይህ መግለጫ ምናልባት እስራኤላውያን ስለ ነበራቸው ጥቂት የጦር መሣሪያ በግነት የቀረበ ይሆናል። አ.ት፡ “በእስራኤል ለጦርነት የቀረው ጥቂት የጦር መሣሪያ ነው” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

በእስራኤል አርባ ሺህ

“40,000 በእስራኤል” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 5:9

ልቤ ወደ እስራኤል አዛዦች ይሄዳል

“ልብ” የሚለው ቃል የአንድን ሰው ስሜት ይወክላል። “ልቤ ይሄዳል” የሚለው ሐረግ ዲቦራ ያላትን አድናቆት ወይም ምስጋና የማመልከቻ መንገድ ነው። አ.ት፡ “የእስራኤልን አዛዦች አደንቃለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እናንተ በነጫጭ አህዮች የምትቀመጡ - በመንገዱ ላይ የምትሄዱ

ይህ ንጽጽር የሚያመለክተው ምናልባት ባለጸጎችንና ድኾችን ይሆናል። አ.ት፡ “እናንት በነጫጭ አህዮች የምትቀመጡ ባለጸጎች … እናንት በመንገዱ ላይ የምትሄዱ ድኾች”

ለኮርቻ በስጋጃዎች ላይ ተቀምጣችሁ

እነዚህ ስጋጃዎች ምናልባት ጋላቢው በይበልጥ እንዲመቸው በአህያው ጀርባ ላይ ለኮርቻነት የሚጠቀምባቸው ሳይሆኑ አይቀሩም።

Judges 5:11

የእነዚያን ድምፆች ስሙ

እዚህ ጋ “ድምፆች” የሚዘምሩትን ሰዎች ይወክላል። አ.ት፡ “ስሟቸው”

ወደ ከተማይቱ በሮች ወረዱ

እዚህ ጋ “በሮች” መላውን ከተማ ይወክላሉ። አ.ት፡ “ወደ ከተሞቻቸው ተመለሱ”

Judges 5:12

ንቂ፣ ንቂ

ተናጋሪዎች ሊሆኑ የሚችሉት 1) የእስራኤል ሕዝብ ወይም 2) ለራሷ የምትናገረው ዲቦራ ወይም 3) መዝሙሩን የጻፈው ገጣሚ ነው።

ዲቦራ

ይህንን ስም በመሳፍንት 4፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ባርቅ - አቢኒኤም

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 4፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ከጦረኞች ጋር ወደ እኔ

“እኔ” የሚለው ቃል ዲቦራን ያመለክታል።

Judges 5:14

ሥሩ በአማሌቅ ከሆነው ከኤፍሬም

የኤፍሬም ሰዎች የሚኖሩበት ምድር በመጀመሪያ የአማሌቅ ተወላጆች ይኖሩበት ስለ ነበረ የኤፍሬም ሰዎች በምድሪቱ እንደ ተተከሉና ስር እንደ ሰደዱ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “በአንድ ወቅት የአማሌቅ ተወላጆች ይኖሩ ከነበሩበት ከኤፍሬም ምድር” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ተከተሉህ

እዚህ ጋ “ተከተሉህ” የሚያመለክተው የኤፍሬምን ሕዝብ ነው። በሦስተኛ መደብ ሊነገር ይቻላል። አ.ት፡ “ተከተሏቸው” (የአንተ ቅርጾች እና አንደኛ፣ ሁለተኛ፣ ወይም ሦስተኛ መደብ የሚለውን ተመልከት)

ማኪር

ይህ የማኪር ተወላጆች ይኖሩ የነበሩበት ስፍራ ነው። ማኪር የምናሴ ልጅና የዮሴፍ የልጅ ልጅ ነበር። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከዛብሎን፣ እነዚያ የአለቅነትን በትር የያዙ

ወታደራዊ አመራሮች የስልጣናቸው ምልክት በሆነው በትራቸው ይገለጻሉ። አ.ት፡ “የዛብሎን ወታደራዊ መሪዎች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 5:15

በይሳኮር ያሉ መስፍኖቼ ከዲቦራ ጋር ነበሩ

እዚህ ጋ “የእኔ” የሚያመለክተው ዲቦራን ነው። ይህ መግለጫ በአጠቃላይ በአንደኛ መደብ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በይሳኮር የሚገኙት መስፍኖቼ ከእኔ ጋር ነበሩ” (አንደኛ፣ ሁለተኛ፣ ወይም ሦስተኛ መደብ የሚለውን ተመልከት)

ዲቦራ

ይህንን ስም በመሳፍንት 4፡4 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

ይሳኮር ከባርቅ ጋር ነበር

እዚህ ጋ “ይሳኮር” የይሳኮርን ነገድ ያመለክታል። አ.ት፡ “የይሳኮር ነገድ ከባርቅ ጋር ነበር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ባርቅ

ይህንን ስም በመሳፍንት 4፡6 እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

መመሪያውን በመከተል ከበስተኋላው ወደ ሸለቆው ሮጡ

“መመሪያውን በመታዘዝና ወደ ሸለቆው ከበስተኋላው በመሮጥ”

ከበስተኋላው በመሮጥ

“ከኋላው በመከተል” ወይም “ከኋላው በመሮጥ”

ታላቅ የልብ ምርምር ነበር

እዚህ ጋ “ልብ” አሳብን ይወክላል። የሰዎቹ እርስ በእርስ መነጋገርና ምን ማድረግ እንዳለባቸው መወሰን አለመቻላቸው ልባቸውን እንደመረመሩ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ምን ማድረግ እንዳለባቸው ብዙ ውይይት ነበር” (ፈሊጣዊ እና ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 5:16

እረኞች ለመንጋዎቻቸው የሚጫወቱትን ዋሽንት እየሰማችሁ እሳት በሚነድባቸው ምድጃዎች መካከል የተቀመጣችሁት ለምንድነው?

ወደ ጦርነቱ በመምጣት ለመዋጋት አልወሰኑም ነበርና ይህ ጥያቄ የተጠየቀው የሮቤልን ሰዎች ለመውቀስ ነው። ይህ እንደ መግለጫ ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በቤት ቀርታችሁ እረኞች ለመንጋዎቻቸው የሚጫወቱትን ዋሽንት ከምትሰሙ ይልቅ ስንዋጋ ልትረዱን ይገባ ነበር” (መልስ የማይሻ ጥያቄ እና የሚለውን ተመልከት)

እሳት የሚነድባቸው ምድጃዎች

አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ዕትሞች “የበጎች ጉረኖ” ወይም “የበግ ማሳደሪያ” ይሉታል

Judges 5:17

ገለዓድ ተቀምጧል

እዚህ ጋ “ገለዓድ” የሚያመለክተው በጦርነቱ ላይ ለመዋጋት መሄድ የነበረባቸውን የገለዓድ ወንዶች ነው። አ.ት፡ “የገለዓድ ሰዎች ተቀምጠዋል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከዮርዳኖስ ማዶ

ይህ የዮርዳኖስን ምስራቅ ያመለክታል።

ዳን በመርከቦች ላይ ለምን ዘገየ

የዳን ነገድ ሰዎች ለእስራኤል ስላልተዋጉ ይህ ጥያቄ የተጠየቀው ቁጣን ለመግለጽ ነው። አ.ት፡ “የዳን ሰዎች በመርከቦቻቸው ውስጥ መቆየት አልነበረባቸውም” ወይም “በጦርነቱ የዳን ነገድ ሰዎች አልረዱንም። ይልቁንም በመርከቦቻቸው ውስጥ ሆነው ወዲያና ወዲህ ይቅበዘበዙ ነበር!” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ እና የሚለውን ተመልከት)

ለምን ነበር ዳን

እዚህ ጋ “ዳን” ጦርነቱን ለመዋጋት መሄድ የነበረባቸውን የዳን ሰዎች ይወክላል። አ.ት፡ “ለምንድነው የዳን ሰዎች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በመርከቦች የሚቅበዘበዙት

የዳን ነገድ የሚገኘው በሜዴትራንያን ባህር አጠገብ ነበር። በንግድና ዓሳ በማስገር ገንዘብ ለማግኘት በባህሩ ላይ በመርከብ ይጓዙ ነበር።

አሴር በጠረፉ ላይ ተቀመጠ፣ በወደቡም አቅራቢያ ኖረ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉሙ በይበልጥ ሊብራራ ይችላል። አ.ት፡ “የአሴር ነገድ ሰዎችም ደግሞ ሳይረዱን ቀሩ። በወደቦቻቸው አቅራቢያ ብቻ ተቀመጡ”

አሴር ተቀመጠ

እዚህ ጋ “አሴር” ጦርነቱን ለመዋጋት መሄድ የነበረባቸውን የአሴር ሰዎች ይወክላል። አ.ት፡ “የአሴር ሰዎች ተቀመጡ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወደቦች

ጥልቅ ውሃ ያለባቸውና መርከቦች የሚቆሙባቸው የባህር ዳርቻ አካባቢዎች

ንፍታሌምም ደግሞ

የሚታወቀውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “ንፍታሌምም ደግሞ ነፍሳቸውን እስከ ሞት ድረስ አሳልፈው ከሰጡት ነገዶች አንዱ ነበር”

Judges 5:19

ነገሥታት መጡ፣ ተዋጉም - የከነዓን ነገሥታት ተዋጉ

ራሱንና የሚያዛቸውን ሰራዊት ለማመልከት የአንድ ሕዝብ ወገን ንጉሥ የሚለው ጥቅም ላይ ውሏል። አ.ት፡ “ነገሥታትና ሰራዊቶቻቸው መጥተው ተዋጉ - የከነዓን ነገሥታትና ሰራዊቶቻቸው ተዋጉ”

እነርሱ ተዋጉ -- ተዋጉ

“እኛ” የሚለው ቃል የሚታወቅ ነው። አ.ት፡ “ወጉን - ወጉን”

ታዕናክ - መጊዶ

የእነዚህን ቦታዎች ስም በመሳፍንት 1፡27 እንዳደረግኸው ተርጉማቸው።

ምንም ብር አልበዘበዙም

እዚህ ጋ “ብር” በጥቅሉ የትኛውንም ዓይነት ገንዘብ ይወክላል። አ.ት፡ “የሚበዘብዙት ብር ወይም ሌላ ሀብት አልነበረም”

ብዝበዛ

አብዛኛውን ጊዜ በጦርነት ወይም በሌቦች አማካይነት በማስገደድ የሚወሰዱ ነገሮች

ከዋክብት ከሰማይ ተዋጉ፣ ከሰማያት ጥጎቻቸው ሲሣራን ተዋጉት

እግዚአብሔር፣ እስራኤላውያን ሲሣራንና ሰራዊቱን ድል እንዲያደርጓቸው መርዳቱ ከዋክብት ራሳቸው ሲሣራንና ሰራዊቱን እንደተዋጓቸው ተደርጎ ተነግሯል። ይህ እግዚአብሔር ሲሣራን ድል ለማድረግ ተፈጥሮአዊ ግብዓቶችን በተለይም ነጎድጓድን መጠቀሙን ያመለክት ይሆናል። (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

በሲሣራ ላይ

እዚህ ጋ “ሲሣራ” የሚወክለው ራሱንና መላውን ሰራዊቱን ነው። አ.ት፡ “ሲሣራና ሰራዊቱ”

ሲሣራ

ይህንን ስም በመሳፍንት 4፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Judges 5:21

የቂሶን ወንዝ ጠራርጎ ወሰዳቸው

በከባድ ዝናብ ምክንያት ወንዙ በፍጥነት ስለሞላ ሠረገላዎቹ በጭቃ ተይዘው ስለነበር ብዙ ወታደሮች ሰመጡ። አ.ት፡ “የቂሶን ወንዝ ጎረፈና የሲሣራን ወታደሮች ጠራርጎ ወሰዳቸው”

ቂሶን

ይህንን በመሳፍንት 4፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ነፍሴ ሆይ፣ በርቺ፣ ተሰለፊ

እዚህ ጋ “ነፍስ” የሰውን ሁለንተና ያመለክታል። “የእኔ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ዲቦራን ነው። አ.ት፡ “እንድበረታና እንድሰለፍ ለራሴ እነግራለሁ”

ከዚያም የሚጋልቡ የፈረሶች ኮቴ ድምፅ ተሰማ፣ የኃያላኑ ግልቢያ

ይህ የሚገልጸው ከጦርነት የሚሸሹ የብዙ ፈረሶችን ድምፅ ነው። አ.ት፡ “ከዚያም በሽሽት ላይ ያሉ የፈረሶችን ድምፅ ሰማሁ። ብርቱዎቹ የሲሣራ ፈረሶች እየሸሹ ነበር”

መጋለብ

በፍጥነት መሮጥ

Judges 5:23

ሜሮዝን እርገሙ

እዚህ ጋ “ሜሮዝ” የምትወክለው በዚያ የኖሩትን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “የሜሮዝን ሰዎች እርገሙ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሜሮዝ

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ነዋሪዎች

በአንድ ስፍራ የሚኖሩ ሰዎች

Judges 5:24

ኢያዔል

ይህንን ስም በመሳፍንት 4፡18 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሔቤር

ይህንን ስም በመሳፍንት 4፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ቄናዊ

የዚህን የሕዝብ ወገን ስም በመሳፍንት 1፡16 ላይ እንዳደረግኸው ተርጉመው።

ቅቤ አመጣችለት

እዚህ ጋ “ቅቤ” የሚያመለክተው የረጋውን ወተት ነው። ይህ በኢያዔል ሰዎች መካከል የተመረጠ ወተትና ተወዳጅ መጠጥ ነበር። አ.ት፡ “እርጎ አመጣችለት” ወይም “የረጋ ወተት አመጣችለት”

ለልዑላን የተገባውን ማዕድ

ለልዑላን ምርጥ የሆነው ነገር ይቀርብ ስለነበር ይህ ሐረግ የሚለው ማዕዱ እጅግ ምርጥ መሆኑን ነው።

Judges 5:26

እጇን ወደ ድንኳኑ ካስማ ሰደደች

“ኢያዔል በግራ እጇ የድንኳኑን ካስማ ያዘች”

የድንኳን ካስማ

ይህ ድንኳኑን ከመሬት ጋር አገናኝቶ እንዲይዝ በመዶሻ የሚመታ እንደ ትልቅ ሚስማር የሾለ እንጨት ወይም ብረት ነው። ይህንን በመሳፍንት 4፡21 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ቀኝ እጇን ሠራተኛ ወደሚጠቀምበት መዶሻ

ይህ ሙሉ ዐረፍተ ነገር ሆኖ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “በቀኝ እጇ መዶሻ ያዘች”

መዶሻ

የድንኳኑን ካስማ ወደ መሬት ለማጥለቅ ክብደት ካለው እንጨት የሚሠራ መምቻ ነው። ይህንን በመሳፍንት 4፡21 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሲሣራ

የዚህን ሰውዬ ስም በመሳፍንት 4፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት፡

መዛል

ዐቅም ማጣት ወይም መንቀሳቀስ አለመቻል

በቁጣ ተገደለ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ገደለችው” ወይም “ሞተ”(አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 5:28

ርብራብ

ይህ በመስቀልዮሽ እንጨት የተሠራ የመስኮቱ መደገፊያ ነው።

ሠረገላው ሳይመጣ ለምን ይህን ያህል ጊዜ ፈጀበት? ሠረገላዎቹን የሚጎትቱት ፈረሶች ኮቴ ድምፅ ለምን ዘገየ?

ሁለቱም ጥያቄዎች የሚሉት አንድ ነገር ነው። እነዚህ ሁለቱም መግለጫዎች መጣመር ይችላሉ። አ.ት፡ “ሲሣራ ወደ ቤት ሳይመለስ የቆየው ለምንድነው?”

ሠረገላው - ፈጀበት - ሠረገላዎቹን የሚጎትቱት ፈረሶች ኮቴ ድምፅ

ሁለቱም አነጋገሮች የሚወክሉት ሲሣራን ነው። አ.ት፡ “ሲሣራን የወሰዱት. . . እርሱ ለምን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 5:29

ጠቢብ ልዕልቶች

“ልዕልት” የንጉሥ ልጅ ናት፣ ነገር ግን “ልዕልቶች” ማለት ደግሞ ምናልባት የንጉሡን ቤተሰቦች የሚያማክሩ ሴት አማካሪዎች ማለት ሊሆን ይችላል። አ.ት፡ “ጠቢብ ሴቶች”

ለራሷ ተመሳሳይ ምላሽ ሰጠች

“ያንኑ ነገር ለራሷ ተናገረች”

ምርኮ አግኝተው ተከፋፍለው አልጨረሱ ይሆን?

ሴቶቹ በእርግጥ የሆነው ይኸው ነው ብለው ስላመኑበት ጉዳይ አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ይጠቀማሉ። አ.ት፡ “ለመከፋፈል ጊዜ የፈጀባቸው ብዙ ምርኮ እግኝተው መሆን አለበት” (መልስ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ከበዘበዟቸው ላይ - አንድ ማህፀን፣ እያንዳንዱ ሁለት ማህፀን

ሴቶቹ በእርግጥ የሆነው ይኸው ነው ብለው ስላመኑበት ጉዳይ አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ይጠቀማሉ። አ.ት፡ “ከበዘበዟቸው ላይ ለእያንዳንዱ ወንድ አንድ ማህፀን፣ ሁለት ማህፀን ደርሷቸው መሆን አለበት” (መልስ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ለእያንዳንዱ ወንድ አንድ ማህፀን፣ ሁለት ማህፀን

እዚህ ጋ “ማህፀን” የሚያመለክተው ሴትን ነው። የሲሣራ ሰዎች ብዙ ሴቶችን እንደማረኩ የሲሣራ እናት ታምናለች። አ.ት፡ “እያንዳንዱ ወታደር አንድ ወይም ሁለት ሴት ይደርሰዋል”

የቀለመ ጨርቅ

“ልዩ ልዩ ቀለም ያለው ልብስ” ወይም “ልዩ ልዩ ቀለም ያላቸው ልብሶች”

ማቅለም

ልዩ ልዩ ቀለማት ካላቸው ክሮች የተሠሩ ንድፎች

ለሚበዘብዙት ለአንገታቸው

እዚህ ጋ “አንገታቸው” የሚወክለው የሲሣራን ወታደሮች ነው። አ.ት፡ “የበዘበዙት ወታደሮች ሊለብሱት”

Judges 5:31

በብርታቷ እንደምትወጣ ፀሐይ

የየትኛውም ሀገር ሰራዊት የፀሐይን መውጣት ማስቆም ስለማይችል የእስራኤል ሕዝብ እንደ ማለዳ ፀሐይ ለመሆን ይመኛሉ።

ምድሪቱ ሰላም ነበራት

እዚህ ጋ “ምድሪቱ” የሚወክለው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “የእስራኤልም ሕዝብ በሰላም ኖሩ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለአርባ ዓመታት

“ለ40 ዓመታት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)


Chapter 6

1 የእስራኤልም ሕዝብ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን ሥራ ሠሩ፤ እርሱም በምድያም ቁጥጥር ስር እንዲሆኑ ለሰባት ዓመት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ 2 የምድያምም ኃይል በእስራኤል ላይ በረታ፡፡ ከምድያምም የተነሣ የእስራኤል ሕዝብ በኮረብታዎች ላይ ጕድጓድ፣ ዋሻና ምሽግም ለራሳቸው መሸሸጊያ አበጁ። 3 እንዲህም ሆነ፣ እስራኤል ዘር በዘሩ ጊዜ ምድያማውያን፣ አማሌቃውያንና ከምሥራቅም የመጡ ሰዎች እስራኤላውያንን ያጠቁ ነበር፡፡ 4 ሰራዊታቸውን በምድሪቱ ላይ ያሰፍሩና እስከ ጋዛ ድረስ ያለውን ሰብል ያጠፉ ነበር፡፡ በእስራኤልም ምንም መብል፣ በጎች፣ ከብቶችና አህያዎች አይተዉም ነበር፡፡ 5 እነርሱ እንስሶቻቸውንና ድንኳኖቻቸውን ይዘው ሲመጡ እንደ አንበጣ መንጋ ሆነው ይመጡ ነበር፤ እነርሱንና ግመሎቻቸውንም መቁጠር አይቻልም ነበር፡፡ ምድሪቱንም ያጠፉ ዘንድ ይወርሩአት ነበር፡፡ 6 ምድያም እስራኤልን ክፉኛ ከማዳከማቸው የተነሣ የእስራኤል ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፡፡ 7 የእስራኤል ሕዝብ በምድያም ምክንያት ወደ እግዚአብሔር በጮኹ ጊዜ፣ 8 እግዚአብሔር ወደ እስራኤል ልጆች ነቢይ ላከ፡፡ ነቢዩም እንዲህ አለ፡- “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡- ‘እኔ ከግብፅ ምድር አወጣኋችሁ፤ ከባርነትም ቤት አወጣኋችሁ፡፡ 9 ከግብፃውያንም እጅ እንደዚሁም ይጨቁኑአችሁ ከነበሩ ኃይላት ሁሉ አዳንኋችሁ፡፡ ከፊታችሁም አሳድጄ አወጣኋቸው፣ ምድራቸውንም ሰጠኋችሁ፡፡ 10 ለእናንተንም እንዲህ አልኋችሁ፣ “እኔ አምላካችሁ እግዚአብሔር ነኝ፤ በምድራቸው የተቀመጣችሁባቸውን፣ የአሞራያውያንን አማልክት እንዳታመልኩ አዘዝኋችሁ፡፡ ነገር ግን እናንተ ድምጼን አልታዘዛችሁም፡፡ 11 የእግዚአብሔርም መልአክ መጣና በዖፍራ ባለችው ለአቢዔዝራዊው ለኢዮአስ በነበረችው ከበሉጥ ዛፍ በታች ተቀመጠ፤ የኢዮአስም ልጅ ጌዴዎን ከምድያማውያን ለመሸሸግ በወይን መጥመቂያው ውስጥ ስንዴ ይወቃ ነበር፡፡ 12 የእግዚአብሔርም መልአክ ለእርሱ ተገልጠለትና እንዲህ አለው፣ “አንተ ብርቱ ተዋጊ ሰው፣ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነው አለው!” 13 ጌዴዎንም ለእርሱ እንዲህ አለው፣ “ጌታዬ ሆይ፣ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ከሆነ፣ ይህ ነገር ሁሉ ለምን በእኛ ላይ ደረሰብን? አባቶቻችንስ የነገሩን እርሱ የሰራቸው አስደናቂ ነገሮች ወዴት አሉ፣ እንዲህ ብለው የነገሩን፣ ‘እግዚአብሔር ከግብፅ አላወጣንምን?’ አሁን ግን እግዚአብሔር ትቶናል፣ ለምድያማውያንም ብርታት አሳልፎ ሰጥቶናል፡፡ 14 እግዚአብሔርም ወደ እርሱ ተመለከተና እንዲህ አለው፣ “በዚህ ባለህ ብርታት ሂድ፡፡ እስራኤልንም ከምድያም ኃይል አድን፤ እነሆ እኔ አልላክሁህምን?” 15 ጌዴዎንም እንዲህ አለው፣ “ጌታ ሆይ፣ እባክህ፣ እኔ እስራኤልን እንዴት ማዳን እችላለሁ? ተመልከት፣ የእኔ ቤተሰብ ከምናሴ ነገድ ከሁሉ ይልቅ ደካማ ነው፣ እኔም በአባቴ ቤት ውስጥ የመጨረሻ ነኝ፡፡ 16 እግዚአብሔርም፣ “እኔ ከአንተ ጋር እሆናለሁ፣ አንተም የምድያምን ሰራዊት በሙሉ ታሸንፋለህ” አለው፡፡ 17 ጌዴዎንም እንዲህ አለው፣ “በእኔ ደስተኛ ከሆንህ፣ የምትናገረኝ አንተ እንደሆንህ እርግጠኛ እሆን ዘንድ ምልከትን ስጠኝ፡፡ 18 ወደ አንተ እስክመጣና መስዋእቴን አምጥቼ በፊትህ እስካቀርብ ድረስ እባክህ ከዚህ አትሂድ፡፡” እግዚአብሔርም “እስክትመለስ ድረስ እቆያለሁ” አለ፡፡ 19 ጌዴዎን ሄደ የፍየሉንም ጠቦት አረደ፣ የኢፍ መስፈሪያም ዱቄት ወስዶ ያልቦካ ቂጣ አዘጋጀ፡፡ ሥጋውን በቅርጫት አኖረ፣ መረቁንም በምንቸት ውስጥ አኖረ፣ ሁሉንም ይዞ በበሉጥ ዛፍ በታች አቀረበለት፡፡ 20 የእግዚአብሔርም መልአክ እንዲህ አለው፣ “ሥጋውንና ያልቦካውን ቂጣ ውሰድና በዚህ ድንጋይ ላይ አኑረው፣ መረቁንም በላዩ ላይ አፍስሰው፡፡” ጌዴዎንም እንዲሁ አደረገ፡፡ 21 የእግዚአብሔርም መልአክ በእጁ የያዘውን የበትሩን ጫፍ ወደዚያ ዘረጋ፡፡ በበትሩም ሥጋውንና ያልቦካውን ቂጣ ነካው፤ እሳትም ከድንጋዩ ውስጥ ወጥቶ ሥጋውንና ያልቦካውን ቂጣ በላ፡፡ የእግዚአብሔርም መልአክ ሄደ፣ ጌዴዎንም ሊያየው አልቻለም፡፡ 22 ጌዴዎንም የእግዚአብሔር መልአክ እንደ ሆነ አወቀ፡፡ ጌዴዎንም፣ “አምላኬ እግዚአብሔር ሆይ፣ ወዮልኝ! የእግዚአብሔርን መልአክ ፊት ለፊት አይቻለሁና” አለ፡፡ 23 እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፣ “ሰላም ለአንተ ይሁን! አትፍራ፣ አትሞትም፡፡” 24 ስለዚህ ጌዴዎን በዚያ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሠራ፡፡ ስሙንም፣ እግዚአብሔር ሰላም ብሎ ጠራው፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ በአቢዔዝራውያን ጎሳ በምትሆነው በዖፍራ አለ፡፡ 25 እግዚአብሔርም በዚያች ሌሊት እንዲህ አለው፣ “የአባትህን በሬ፣ ሰባት ዓመት የሆነውን ሁለተኛውንም በሬ ውሰድ፣ የአባትህ የሆነውን የበኣል መሠዊያ አፍርስና በአጠገቡ ያለውን አሼራን ሰባብረው፡፡ 26 በዚህ መሸሸጊያ ስፍራ ጫፍ ላይ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሥራ፣ በትክክለኛው መንገድም ስራው፡፡ ከአሼራ ሰባብረህ በጣልኸው እንጨት ሁለተኛውን በሬ የሚቃጠል መስዋእት አድርገህ አቅርበው፡፡” 27 ስለዚህ ጌዴዎን ከባሪያዎቹ አሥር ሰዎችን ወሰደና እግዚአብሔር እንደነገረው አደረገ፡፡ ነገር ግን በቀን ለማድረግ የአባቱን ቤተ ሰቦችና የከተማውንም ሰዎች እጅግ በጣም ስለፈራ፣ በሌሊት አደረገው፡፡ 28 በማለዳ የከተማው ሰዎች በተነሱ ጊዜ፣ የበኣል መሠዊያ ፈርሶ ነበር፣ በአጠገቡ የነበረውም አሼራ ተሰባብሮ ነበር፣ ሁለተኛውም በሬ አዲስ በተሰራው መሠዊያ ላይ ተሠውቶ ነበር፡፡ 29 የከተማውም ሰዎች እርስ በርሳቸው፣ “ይህን ያደረገው ማን ነው?” ተባባሉ፡፡ ከሌሎች ጋር ሲነጋገሩና መልስ ሲፈልጉ ሳሉ፣ “ይህን ያደረገው የኢዮአስ ልጅ ጌዴዎን ነው” አሉ፡፡ 30 የዚያን ጊዜ የከተማው ሰዎች ኢዮአስን እንዲህ አሉት፣ “የበኣልን መሠዊያ አፍርሶአልና፣ በአጠገቡ የነበረውንም አሼራ ሰባብሮታልና እንዲሞት ልጅህን አውጣ፡፡” 31 ኢዮአስም ለተቃወሙት በሙሉ እንዲህ አላቸው፣ “ለበኣል ትምዋገቱለታላችሁን? እርሱን ታድኑታላችሁን? ለእርሱ የሚምዋገትለት ሁሉ እስከ ነገ ጠዋት ይገደል፡፡ በኣል አምላክ ከሆነ፣ መሠዊያውን ሲያፈርሱበት ራሱን ይከላከል፡፡ 32 ስለዚህም በዚያ ቀን ጌዴዎን “ይሩበኣል” የሚል ስም ተሰጠው፣ ምክንያቱም እርሱ “በኣል ራሱን ይከላከል” ብሏልና፣ ጌዴዎን መሠዊያውን አፍርሶአልና፡፡ 33 ምድያማውያንና አማሌቃውያን ሁሉ፣ የምሥራቅም ሰዎች አንድ ላይ ተሰበሰቡ፡፡ ዮርዳኖስን ተሻግረው በኢይዝራኤል ሸለቆ ውስጥ ሰፈሩ፡፡ 34 ነገር ግን የእግዚአብሔር መንፈስ ጌዴዎንን ሊረዳው በእርሱ ላይ ወረደ፡፡ ጌዴዎንም ቀንደ መለከት ነፋ፣ የአቢዔዝር ጎሳ ሰዎች ይከተሉት ዘንድ ጠራቸው፡፡ 35 እርሱም ወደ ምናሴ ነገድ ሁሉ መልክተኞችን ሰደደ፣ እነርሱም ደግሞ እንዲከተሉት ተጠርተው ነበር፡፡ መልክተኞችንም ወደ አሴር፣ ዛብሎንና ንፍታሌምም ላከ፣ እነርሱም እርሱን ሊየገኙት ሄዱ፡፡ 36 ጌዴዎንም እግዚአብሔርን እንዲህ አለው፣ “እንደ ተናገርኸው እስራኤልን ለማዳን እኔን የምትጠቀምብኝ ከሆነ 37 ተመልከት፣ በአውድማው ላይ የበግ ጠጕር ባዘቶ አኖራለሁ፡፡ በጠጕሩ ብቻ ላይ ጠል ቢሆንና በምድሩም ሁሉ ደረቅ ቢሆን፣ የዚያን ጊዜ እንደተናገርኸው አንተ እስራኤልን ለማዳን እንደምትጠቀምብኝ አውቃለሁ፡፡” 38 እንዲሁም ሆነ፣ ጌዴዎን በነጋው ማልዶ ተነሣ፣ ጠጕሩንም በአንድ ላይ ጨመቀው፣ ከጠጕሩም የተጨመቀው ጠል አንድ ቆሬ ለመሙላት በቂ ሆነ፡፡ 39 ጌዴዎንም እግዚአብሔርን እንዲህ አለው፣ “አትቈጣኝ፣ አንድ ጊዜ እንደገና እናገራለሁ፡፡ እባክህ፣ የጠጉሩ ባዘቶ በመጠቀም አንድ ተጨማሪ ሙከራ እንዳደርግ ፍቀድልኝ፡፡ በዚህ ጊዜ ጠጕሩ ብቻ ደረቅ ይሁን፣ በምድሩና በዙርያውም ሁሉ ላይ ደግሞ ጠል ይሁን፡፡” 40 እግዚአብሔርም በዚያ ሌሊት የጠየቀውን አደረገ፡፡ ጠጕሩ ደረቅ ነበረ፣ በምድሩም ሁሉ ላይ ጠል ነበረ፡፡



Judges 6:1

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የሚወክለው ፍርዱን ወይም ምዘናውን ነው። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ፍርድ ክፉ የሆነውን” ወይም “እግዚአብሔር ክፉ ነው ያለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የምድያማውያን እጅ

እዚህ ጋ “ምድያማውያን” የሚወክለው የምድያምን ሰዎች ነው። በተጨማሪም፣ “እጅ” መቆጣጠርን ይወክላል። አ.ት፡ “የምድያም ሰዎች መቆጣጠራቸው” ወይም “የምድያማውያን መቆጣጠር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የምድያም ኃይል እስራኤልን አስጨነቀ

እዚህ ጋ “የምድያም ኃይል” የሚያመለክተው የምድያም ሰዎችን ነው። አ.ት፡ “የምድያም ሰዎች ከእስራኤል ሰዎች ይልቅ እጅግ በርትተው ስለነበር አስጨነቋቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ዋሻ

ሊያስጠልል የሚችል በዐለታማ ሸንተረር ላይ የሚገኝ ስፍራ

Judges 6:3

ሰራዊታቸውን ያሰፍሩ ነበር

“ሰራዊቱ ይሰፍር ነበር” ወይም “ሰራዊቱ ድንኳኑን ይተክል ነበር”

Judges 6:5

እነርሱ ከከብቶቻቸውና ከድንኳኖቻቸው ጋር ወጥተው በሚመጡበት ጊዜ ሁሉ

የምድያም ምድር በቀይ ባህር አቅራቢያ ከእስራኤል ምድር በስተደቡብ ነበር። ከምድያም ወደ እስራኤል የሚደረግ ጉዞ በሚነገርበት ጊዜ “ወጥተው በሚመጡበት” የሚለውን ሐረግ መጠቀም የተለመደ ነበር። አ.ት፡ “ምድያማውያን ከብቶቻቸውንና ድንኳኖቻቸውን ወደ እስራኤል ምድር በሚያመጡበት ጊዜ ሁሉ”

እንደ አንበጣ መንጋ ይመጡ ነበር

ምድያማውያን እጅግ ብዙ ሆነው ይመጡ ስለነበርና ከብቶቻቸው የሚበቅለውን ነገር ሁሉ ይበሉት ስለነበር ከአንበጣ መንጋ ጋር ተነጻጽረዋል።

ለመቁጠር አይቻልም ነበር

ይህ ቁጥሩ በጣም ብዙ መሆኑን ለማሳየት የቀረበ ግነት ነው። (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

ምድያም አደከማቸው

እዚህ ጋ “ምድያም” የሚወክለው የምድያምን ሕዝብ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወደ እግዚአብሔር ጮኹ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንዲረዳቸው ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:7

ወደ እግዚአብሔር ጮኹ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንዲረዳቸው ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በምድያም ምክንያት

እዚህ ጋ “ምድያም” የሚወክለው የምድያምን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “በምድያማውያን ምክንያት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከግብፅ አወጣዃችሁ

“ከግብፅ መርቼ አወጣዃችሁ”

ከባርነት ቤት

ሙሴ ስለ ግብፅ ሲናገር ሰዎች ባሪያዎችን እንደሚያቆዩበት ቤት ይቆጥረዋል። አ.ት፡ “ባሪያዎች የነበራችሁበት ስፍራ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:9

ከ… እጅ

በዚህ ሐረግ “እጅ” የሚወክለው ኃይልን ወይም ቁጥጥርን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ድምፄን አልታዘዛችሁም

እዚህ ጋ “ድምፄን” የሚወክለው እግዚአብሔር ያዘዘውን ትዕዛዝ ነው። አ.ት፡ “ትዕዛዜን አልጠበቁም” ወይም “አልታዘዙኝም”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:11

አሁን

ይህ ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የታሪኩ መስመር የተገታበትን ለማመልከት ነው። ተራኪው እዚህ ጋ የታሪኩን አዲስ ክፍል መናገር ይጀምራል።

ዖፍራ

ይህ የከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አቢዔዝራዊ

ይህ በቀድሞ አባታቸው በአቢዔዝር ስም የሚጠሩ የሕዝብ ወገን ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ወለሉ ላይ ስንዴ ይወቃ ነበር

ይህ የ “መውቃት” ሂደት ነው። ጌዴዎን የስንዴውን ምርት ከገለባው ለመለየት ወለሉ ላይ ይወቃ ነበር”

ታየው

“ወደ እርሱ ሄደ”

Judges 6:13

ጌታዬ

ጌዴዎን “ጌታዬ” የሚለውን ቃል የሚጠቀመው እንግዳ የሆነን ሰው በትህትና ሰላምታ ለመስጠት ነው። እርሱ የሚናገረው በመልአክ ወይም በሰው መልክ ከታየው ከእግዚአብሔር ጋር እንደሆነ አልተገነዘበም።

‘እግዚአብሔር ከግብፅ ያወጣን አይደለምን?’ ብለው አባቶቻችን የነገሩን ተአምራቱ ሁሉ የት አለ?

እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር እንዳለ የነገረውን እንግዳ ለመገዳደር ጌዴዎን ጥያቄ ያቀርብለታል። ደግሞም፣ በቀጥታ የተጠቀሰው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ ባልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር አባቶቻችንን ከግብፅ ባወጣቸው ጊዜ ስላደረገላቸው የነገሩንን ዓይነት ተአምር አንድም አላየንም”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ፣ ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

በምድያማውያን እጅ ሰጥቶናል

“በ… ሰጥቶናል” የሚለው ሐረግ እስራኤላውያን እንዲሸነፉ እግዚአብሔር ፈቅዷል ማለት ነው። አ.ት፡ “ምድያማውያን እንዲያሸንፉን ፈቅዷል”

በ… እጅ ሰጥቶናል

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ኃይልን ወይም ቁጥጥርን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በምድያም

እዚህ ጋ “ምድያም” የሚወክለው የምድያምን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “በምድያማውያን”(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:14

እግዚአብሔር ወደ እርሱ ተመልክቶ

“እግዚአብሔር ወደ ጌዴዎን ተመልክቶ”

ከ… እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ኃይልን ወይም ቁጥጥርን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የምድያም

እዚህ ጋ “ምድያም” የሚወክለው የምድያምን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “በምድያማውያን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አልላክሁህምን?

እግዚአብሔር ጌዴዎንን እንደ ላከው ለማስረገጥ በጥያቄ መልክ ይጠቀማል። እዚህ ጋ “መላክ” ማለት እግዚአብሔር ጌዴዎንን ለአንድ ግልጽ ለሆነ ሥራ ሾሞታል ማለት ነው። አ.ት፡ “የምልክህ እኔ እግዚአብሔር ነኝ!” (መልስ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ጌታው፣ እባክህን

አሁን ጌዴዎን ሰውየውን በመሳፍንት 6፡13 ላይ እንዳደረገው “ጌታዬ” ከማለት ይልቅ “ጌታው” ብሎ ይጠራዋል። እዚህ ጋ ጌዴዎን እየተነጋገረ ያለው ከእግዚአብሔር ጋር መሆኑን ያወቀ ወይም የጠረጠረ ይመስላል።

እንዴት እስራኤልን ነጻ ማውጣት እችላለሁ?

ጌዴዎን እስራኤላውያንን መታደግ እንደሚችል እንደማያስብ አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ያቀርባል። አ.ት፡ “እስራኤላውያንን በፍጹም ልታደጋቸው አልችልም!” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ቤተሰቤን ተመልከት

“እኔንና ቤተሰቤን ተመልከትና ትክክል መሆኔን ታያለህ”

ከምናሴ

“ከምናሴ ነገድ ውስጥ”

በአባቴ ቤት ውስጥ

እዚህ ጋ “ቤት” የሚወክለው ቤተሰብን ነው። አ.ት፡ “በአባቴ ቤተሰብ ውስጥ“ ወይም “በቤተሰቤ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:16

እኔ ከአንተ ጋር እሆናለሁ

እዚህ ጋ “ከአንተ ጋር” የሚለው ሐረግ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን እግዚአብሔር ጌዴዎንን ይረዳዋል፣ ይባርከዋልም ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እንደ አንድ ሰው

ሙሉውን ትርጉም በይበልጥ ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “ከአንድ ሰው ጋር የምትዋጋውን ያህል በቀላሉ”

በፊትህ አድርግ

“በፊት ለፊትህ አድርገው”

Judges 6:19

የኢፍ መስፈሪያ ዱቄት

ዘመናዊ መስፈሪያ መጠቀም ካስፈለገ ይህን ማድረግ የሚቻልበት አንድ መንገድ አለ። አ.ት፡ “ከ22 ሊትር ዱቄት ጋር”

መረቅ

እንደ ሥጋ ያለ የተቀቀለ ምግብ ያለበት ውሃ።

አቀረበለት

“ለእግዚአብሔር መልአክ አቀረበለት”

የእግዚአብሔር መልአክ

ይህ ከእግዚአብሔር መልአክ ጋር አንድ ነው። አ.ት፡ “በመልአክ መልክ የተገለጠ አግዚአብሔር” ወይም “እግዚአብሔር”

Judges 6:21

የእግዚአብሔር መልአክ

በ6፡11-24 እግዚአብሔር በመልአክ መልክ ለጌዴዎን ተገልጦለታል። ይህንን በመሳፍንት 6፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ተለይቶት ሄደ

“ተሰወረበት”

Judges 6:22

የእግዚአብሔር መልአክ

በ6፡11-24 እግዚአብሔር በመልአክ መልክ ለጌዴዎን ተገልጦለታል። ይህንን በመሳፍንት 6፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ጌታ እግዚአብሔር ሆይ!

እዚህ ጋ “ሆይ” የሚለው ቃል ጌዴዎን እጅግ መፍራቱን ያሳያል።

የእግዚአብሔርን መልአክ ፊት ለፊት አይቻለሁና

ይህ ሐረግ ለእርስ በእርሳቸው ቅርበት ያላቸውን ሁለት ሰዎች ያመለክታል። አ.ት፡ “በእርግጥ የእግዚአብሔርን መልአክ አይቻለሁ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር አለው

እግዚአብሔር ጌዴዎንን ከሰማይ ተናገረው።

እስከዚህ ቀን ድረስ

ይህ ማለት መጽሐፈ መሳፍንት የተጻፈበት ጊዜ ማለት ነው።

ዖፍራ

የዚህን ከተማ ስም በመሳፍንት 6፡11 እንዳደረግከው በተመሳሳይ ተርጉመው።

የአቢዔዝር ጎሳ

የዚህን የሕዝብ ወገን ስም በመሳፍንት 6፡11 እንዳደረግከው ተርጉመው።

Judges 6:25

ሁለተኛውን ወይፈን

“ሁለተኛው” የሚለው ቃል የመቁጠሪያ ቁጥር “ሁለት” ነው። አ.ት፡ “ሌላ ወይፈን”

በአጠገቡ ያለውን

“በበኣል መሠዊያ አጠገብ ያለውን”

በዚህ የመደበቂያ ቦታ አናት ላይ

የዖፍራ ከተማ በኮረብታ አናት ላይ ነበረች። እስራኤላውያን ከምድያማውያን ለመደበቅ ወደዚያ ሸሹ።

በትክክለኛው መንገድ ሥራው

“ድንጋዮቹን ሥርዓት ባለው መልኩ አስቀምጣቸው” ወይም “በአግባቡ አነባብረው”

Judges 6:27

እግዚአብሔር እንደነገረው አደረገ

ይህ እግዚአብሔር በመሳፍንት 6፡25-26 ላይ የሰጠውን ትዕዛዝ ያመለክታል።

Judges 6:28

ተነሣ

“ከአልጋው ተነሣ” ወይም “ነቃ”

የበኣል መሠዊያ ፈርሶ፣ በአጠገቡ የነበረው የአሼራ ምስልም ተሰባብሮና ሁለተኛው ወይፈን በተሠራው መሠዊያ ላይ ተሠውቶ ነበር

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው የበኣልን መሠዊያ እንዳፈረሰ፣ በአጠገቡ የነበረውን የአሼራን ምስል እንደሰባበረውና መሠዊያ ሠርቶ በእርሱ ላይ ሁለተኛውን ወይፈን እንደ ሠዋ አስተዋሉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:30

መሞት አለበት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በሞት ልንቀጣው ይገባናል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:31

ለበኣል ትሟገቱለታላችሁ?

ኢዮአስ ሰው ለአምላክ ጠበቃ መሆን እንደማይኖርበት አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ያቀርብላቸዋል። አ.ት፡ “ለበኣል ጠበቃ ልትሆኑት አይገባም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ትሟገቱለታላችሁ

“ትከላከሉለታላችሁ” ወይም “ሰበብ ትሰጡለታላችሁ”

ታድኑታላችሁ?

ኢዮአስ ሰው አምላክን መታደግ እንደማይኖርበት አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ያቀርብላቸዋል። አ.ት፡ “በኣልን ማዳን የለባችሁም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ትርጉሙም፣ “በኣል ራሱን ይከላከል” የሚል ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ብሏልና

“ኢዮአስ ብሏልና”

Judges 6:33

አሁን

ይህ ቃል እዚህ ጋ ጥቅም ላይ የዋለው የታሪኩ መስመር መገታቱን ለማመልከት ነው። እዚህ ጋ ተራኪው የታሪኩን አዲስ ክፍል መናገር ይጀምራል።

በአንድነት ተሰበሰቡ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉሙ በይበልጥ መብራራት ይችላል። አ.ት፡ “እንደ ሰራዊት በአንድ ላይ ተሰበሰቡ”

Judges 6:34

በጌዴዎን ላይ መጡበት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ጌዴዎንን ተቆጣጠሩት” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የአቢዔዝር ጎሳ

የዚህን የሕዝብ ወገን ስም በመሳፍንት 6፡11 ላይ በተረጎምከው መልኩ ተርጉመው።

እንዲከተሉት

“ወደ ጦርነት” የሚሉት ቃላት ግልጽ ናቸው። አ.ት፡ “ወደ ጦርነት እንዲከተሉት”

እነርሱም ደግሞ እንዲከተሉት ተጠሩ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እንዲከተሉት ይጠራቸዋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ወደ አሴር፣ ዛብሎንና ንፍታሌም

እነዚህ ሁሉ የእያንዳንዱን ጎሳ ሕዝብ ይወክላሉ። አ.ት፡ “ወደ አሴር፣ ዛብሎንና ንፍታሌም ጎሳ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 6:36

የበግ ጠጉር ባዘቶ

ሱፍነት ያለው የበግ ጠጉር

ጠል

ሌሊት ላይ እጽዋት ላይ የሚቆይ ውሃ

ከዚያም እንደምታድን ዐውቃለሁ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉሙ በይበልጥ መብራራት ይችላል። አ.ት፡ “ይህ ከአንተ ዘንድ ምልክት ይሆናል፣ ከዚያም እንደምታድን ዐውቃለሁ”

Judges 6:38

ጌዴዎን ተነሣ

“ጌዴዎን ከአልጋው ተነሣ”

ጨመቀው

ውሃው እንዲወጣለት አንድን ነገር ጠምዝዞ መጭመቅ


Chapter 7

1 ከዚያም ጌዴዎን የተባለው ይሩበኣልና ከእርሱም ጋር የነበሩ ሕዝብ ሁሉ በጠዋት ተነሡ፣ በሐሮድ ምንጭ አጠገብም ሰፈሩ፡፡ የምድያምም ሰፈር ከእነርሱ ወደ ሰሜን በኩል በሞሬ ኮረብታ አጠገብ በሸለቆው ውስጥ ነበረ፡፡ 2 እግዚአብሔርም ጌዴዎንን እንዲህ አለው፣ “ምድያማውያንን እንድታሸንፍ የሚያደርጉህ እጅግ በጣም ብዙ ወታደሮች አሉኝ፡፡ ‘የራሳችን ኃይል አዳነን’ ብለው እስራኤል እንዳይታበዩብኝ እርግጠኛ ሁን፡፡ 3 ስለዚህም አሁን፣ በሕዝቡ ጆሮዎች እንዲህ ብለህ ተናገር፣ “ማንም የፈራ ቢኖር፣ ማንም የደነገጠ ቢኖር፣ የገለዓድን ተራራ ትቶ ይመለስ፡፡” ስለዚህ 22, 000 ሰዎች ተመለሱ፣ 10, 000 ሰዎችም ቀሩ፡፡ 4 እግዚአብሔርም ጌዴዎንን እንዲህ አለው፣ “ሕዝቡ አሁንም ገና ብዙ ነው፡፡ ሕዝቡን ወደ ውኃ ውሰዳቸው፣ በዚያም ቁጥራቸውን ጥቂት አደርግልሃለሁ፡፡ እኔ ‘ይህ ከአንተ ጋር ይሄዳል’ ካልሁህ እርሱ ከአንተ ጋር ይሄዳል፤ ነገር ግን እኔ ‘ይህ ከአንተ ጋር አይሄድም’ ካልሁህ እርሱ ከአንተ ጋር አይሄድም፡፡” 5 ስለዚህ ጌዴዎን ሕዝቡን ወደ ውኃ ወሰዳቸው፣ እግዚአብሔርም ጌዴዎንን እንዲህ አለው፣ “ውሻ እንደሚጠጣ ውኃ የሚጠጣውን ሁሉ፣ ውኃ ለመጠጣት በጕልበታቸው ከሚንበረከኩት ሰዎች መካከል ለይ፡፡” 6 ሦስት መቶ ሰዎች ውኃ እንደ ውሻ ጠጡ፡፡ የቀሩት ሰዎች ግን ውኃ ለጠጡ በጉልበታቸው ተንበረከኩ፡፡ 7 እግዚአብሔርም ጌዴዎንን እንዲህ አለው፣ “ውኃን እንደ ውሻ በጠጡት በሦስት መቶ ሰዎች ከምድያማውያን አድንሃለሁ፣ በእነርሱም ላይ ድል እሰጥሃለሁ፡፡ ሌሎቹ ሰዎች በሙሉ ወደ ስፍራቸው ይመለሱ፡፡” 8 ስለዚህ የተመረጡት ሰዎች ስንቃቸውንና ቀንደ መለከታቸውን ወሰዱ፡፡ ጌዴዎን የእስራኤልን ሰዎች ሁሉ፣ እያንዳንዱን ሰው ወደ ድንኳናቸው ሰደዳቸው፣ ነገር ግን ሦስቱን መቶ ሰዎች በእርሱ ዘንድ አቆያቸው፡፡ የምድያምም ሰፈር ከእርሱ በታች በሸለቆው ውስጥ ነበረ፡፡ 9 በዚያም ሌሊት እግዚአብሔር ለእርሱ እንዲህ አለው፣ “ተነስ! ሰፈራቸውን ምታ፣ በእነርሱ ላይ እኔ ድል እሰጥሃለሁና፡፡ 10 ነገር ግን አንተ ወደ ለመውረድ ከፈራህ፣ ከአገልጋይህ ከፉራ ጋር ወደ ሰፈሩ ውረድ፣ 11 የሚናገሩትንም አድምጥ፣ ከዚያም በኋላ ሰፈሩን ለመውጋት ድፍረት ታገኛለህ፡፡” ስለዚህ ጌዴዎን ከአገልጋዩ ከፉራ ጋር በሰፈሩ ወደ ነበሩት ጠባቂዎች ወረዱ፡፡ 12 ብዛታቸውም እንደ አንበጣ መንጋ የሆነ ምድያማውያን፣ አማሌቃውያንና የምሥራቅም ሰዎች ሁሉ በሸለቆው ውስጥ ሰፍረው ነበር፡፡ የግመሎቻቸውም ብዛት መቁጠር አይቻልም ነበር፤ ቁጥራቸው በባህር ዳርቻ ካለው አሸዋ ይልቅ የሚበልጥ ነበር፡፡ 13 ጌዴዎን በዚያ በደረሰ ጊዜ አንድ ሰው ሕልምን ለጓደኛው ሲነግረው ነበር፡፡ ሰውየውም እንዲህ አለ፣ “ተመልከት! ሕልም አለምሁ፣ አንዲት ክብ የገብስ ቂጣ ወደ ምድያም ሰፈር ተንከባልላ ስትወርድ አየሁ፡፡ ወደ ድንኳኑም ደረሰች፣ እስኪወድቅ ድረስም በጣም መታችው ከዚህ የተነሳ ወደቀ፣ ደግሞም ተገለበጠ፣ ስለዚህም ድንኳኑ ተጋደመ፡፡” 14 ሌላኛውም ሰው እንዲህ አለ፣ “ይህ ነገር ከእስራኤል ሰው ከኢዮአስ ልጅ ከጌዴዎን ሰይፍ በቀር ሌላ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር በምድያምና በሠራዊቱ ሁሉ ላይ ድል ሰጥቶታል፡፡” 15 ጌዴዎን የሕልሙን ዝርዝርና ትርጓሜውን በሰማ ጊዜ በጸሎት ተደፍቶ ሰገደ፡፡ እርሱም ወደ እስራኤል ሰፈር ሄደና እንዲህ አለ፣ “ተነሱ! እግዚአብሔር በምድያም ሠራዊት ላይ ድል ሰጥተአችኋል፡፡” 16 እርሱም ሦስቱን መቶ ሰዎች በሦስት ቡድን ከፈላቸው፣ ለሁሉም ሰዎች ቀንደ መለከትና ባዶ ማሰሮ፣ በማሰሮውም ውስጥ ችቦ ሰጣቸው፡፡ 17 እርሱም እንዲህ አላቸው፣ “እኔን ተመልከቱ፣ የማደርገውንም አድርጉ፡፡ አስተውሉ! ወደ ሰፈሩ ዳርቻ በመጣሁ ጊዜ፣ እኔ የማደርገውን እናንተም ታደርጋላችሁ፡፡ 18 እኔና ከእኔም ጋር ያሉት ሁሉ ቀንደ መለከት ስንነፋ፣ እናንተ ደግሞ በሰፈሩ በሁሉም አቅጣጫ ቀንደ መለከታችሁን ንፉና “ለእግዚአብሔርና ለጌዴዎን” ብላችሁ ጩኹ፡፡ 19 ስለዚህ ጌዴዎንና ከእርሱ ጋር የነበሩት መቶ ሰዎች የመካከለኛው የጥበቃ ሰዓት በተጀመረ ጊዜ ወደ ሰፈሩ ዳርቻ መጡ፡፡ ምድያማውያን የጥበቃ ሰዎችን በሚቀይሩበት ጊዜ፣ ቀንደ መለከቶቹን ነፉ፣ በእጃቸውም የነበሩትንም ማሰሮች ሰባበሩ፡፡ 20 ሦስቱም ቡድኖች ቀንደ መለከቶቹን ነፉ፣ ማሰሮችንም ሰበሩ፡፡ በግራ እጃቸው ችቦችን ያዙ፣ በቀኝ እጃቸው ደግሞ ቀንደ መለከቶችን ይዘው ለመንፋት ተዘጋጁ፡፡ እነርሱም “የእግዚአብሔርና የጌዴዎን ሰይፍ” ብለው ጮኹ፡፡ 21 ሁሉም ሰው በሰፈሩ ዙሪያ በየቦታው ቆመ፣ የምድያማውያን ሠራዊት ሁሉ ሮጡ፡፡ እነርሱም ጮኹና ሸሹ፡፡ 22 ሦስት መቶውንም ቀንደ መለከቶች በነፉ ጊዜ፣ እግዚአብሔር የእያንዳንዱን ምድያማዊ ሰው ሰይፍ በጓደኛውና በራሳቸው ሰራዊት ሁሉ ላይ አዘጋጀ፡፡ ሠራዊቱም በጽሬራ በኩል እስከ ቤትሺጣ፣ በጠባት አጠገብ እስካለው እስከ አቤልምሖላ ዳርቻ ድረስ ሸሸ፡፡ 23 የእስራኤል ሰዎች ከንፍታሌም፣ ከአሴርና ከምናሴም ሁሉ ተሰብስበው ምድያምን ከኋላ እየተከተሉ አሳደዱ፡፡ 24 ጌዴዎን መልክተኞችን በኤፍሬም ወዳለው ኮረብታማ አገር ሁሉ በመስደድ እንዲህ አለ፣ “ምድያምን ለመዋጋት ውረዱና እነርሱን ለማስቆም የዮርዳኖስን ወንዝ እስከ ቤትባራም ድረስ ተቆጣጠሩ፡፡” ስለዚህ የኤፍሬም ሰዎች ሁሉ በአንድ ላይ ተሰብስበው እስከ ቤትባራና ዮርዳኖስ ወንዝ ድረስ ውኃውን ተቆጣጠሩ፡፡ 25 የምድያምን ሁለቱን መሪዎች ሔሬብንና ዜብን ያዙ፡፡ ሔሬብንም በሔሬብ ዓለት ገደሉት፣ ዜብንም በዜብ ወይን መጥመቂያ ላይ ገደሉት፡፡ ምድያማውያንንም አሳደዱ፣ የሔሬብንና የዜብንም ራስ ይዘው በዮርዳኖስ ማዶ ወደነበረው ወደ ጌዴዎን አመጡ፡፡



Judges 7:1

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ስሙን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሰፈሩ

“የጦር ሰፈራቸውን አዘጋጁ”

የሐሮድ ምንጭ - የሞሬ ኮረብታ

እነዚህ የቦታዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የምድያም የጦር ሰፈር በስተሰሜናቸው ነበር

እዚህ ጋ “ምድያም” የሚወክለው የምድያማውያኑን ሰራዊት ነው። አ.ት፡ “የምድያማውያን ሰራዊት የጦር ሰፈራቸውን ከእስራኤላውያን ሰራዊት በስተሰሜን ባለ ስፍራ አደረጉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 7:2

በምድያማውያን ላይ ድል እንድሰጥህ

“ድል” የሚለው ቃል የነገር ስም ሲሆን እንደ ግሥ ወይም ቅጽል ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ምድያማውያንን ታሸንፋቸው ዘንድ እንድፈቅድልህ” ወይም “በምድያማውያን ላይ ባለ ድል ላደርግህ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት”

የገዛ ራሳችን ኃይል አድኖናል

እዚህ ጋ “ኃይል” የሚወክለው ሕዝቡን ራሳቸውን ነው። አ.ት፡ “ያለ እግዚአብሔር እርዳታ ራሳችንን አድነናል” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አሁን

ይህ “በዚህ ሰዓት” ማለት አይደለም፣ ነገር ግን ትኩረትን ወደሚቀጥለው አስፈላጊ ጉዳይ ለመሳብ ጥቅም ላይ ውሏል።

በሕዝቡ ጆሮ ዐውጅ

እዚህ ጋ “ጆሮ” የሰውን ሁለንተና ያመለክታል። አ.ት፡ “ለሕዝቡ ዐውጅ”

ማንም የሚፈራ፣ ማንም የሚንቀጠቀጥ

ሁለቱም ሐረጎች ያላቸው ትርጉም አንድ ነው። (ተመሳሳይነት የሚለውን ተመልከት)

የሚንቀጠቀጥ

ይህ ቃል የሚገልጸው አንድ ሰው ከፍርሐት የተነሣ ሊቆጣጠረው በማይችለው ሁኔታ መንቀጥቀጡን ነው። አ.ት፡ “በፍርሐት የሚንቀጠቀጥ”

ይመለስ

ወዴት እንደሚሄድ ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “ወደ ቤቱ ይመለስ”

ገለዓድ ተራራ

ይህ በገለዓድ አውራጃ የሚገኝ ተራራ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሃያ ሁለት ሺህ

“22,000” (ቁጥሮችን ተመልከት)

አሥር ሺህ ቀሩ

በውስጠ ታዋቂነት “ሰዎች” ወይም “ወንዶች” የሚል ቃል መኖሩን ይረዷል። አ.ት፡ “10,000 ሰዎች ቀሩ” ወይም “10,000 ወንዶች ቀሩ”

አሥር ሺህ

x

Judges 7:4

በዚያ ብዛታቸውን እቀንስልሃለሁ

እዚህ ጋ “ቁጥር” ሰራዊትን ይወክላል። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በበለጠ ግልጽ መሆን ይችላል። አ.ት፡ “በዚያ የሰራዊቱ ቁጥር እንዲቀንስ ማንን ወደ ቤቱ እንደምትመልሰው አሳይሃለሁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የሚለውን ተመልከት)

Judges 7:5

ጌዴዎን አመጣ

“አመጣ” የሚለው ቃል “ወሰደ” ወይም “መራ” ተብሎ ሊተረጎም ይችላል። (ሂድ እና ና የሚለውን ቃል ተመልከት)

በእጆቻቸው

በምላስ በመላስ መጠጣት

ሦስት መቶ ሰዎች

“300 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 7:7

ሦስት መቶ ሰዎች

“300 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አድንሃለሁ፣ ድልንም እሰጥሃለሁ

እዚህ ጋ “አንተ” ብዙ ቁጥር ሲሆን ጌዴዎንና እስራኤላውያንን ያመለክታል።

ስለዚህ እነዚያ የተመረጡት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ስለዚህ እነዚያ እግዚአብሔር የመረጣቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ስንቃቸውንና መለከታቸውን ወሰዱ

እዚህ ጋ “እነርሱ” የሚያመለክተው ሰራዊቱን ትተው የሚመለሱትን የእስራኤል ወታደሮች ነው።

አሁን

ይህ ቃል እዚህ ጋ ጥቅም ላይ የዋለው የታሪኩ መስመር ለአፍታ ቆም ማለቱን ለማመልከት ነው። እዚህ ጋ ተራኪው የታሪኩን አዲስ ክፍል መናገር ይጀምራል።

Judges 7:9

በእነርሱ ላይ ድል ስለምሰጥህ የጦር ሰፈሩን አጥቃ

እዚህ ጋ “የጦር ሰፈር” የሚያመለክተው የምድያማውያንን ሰራዊት በሙሉ ነው። “ድል” የሚለው ቃል የነገር ስም ሲሆን እንደ ግሥ ወይም ቅጽል ሆኖ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እንድታሸንፋቸው ልረዳህ ስለሆነ ምድያማውያንን በጦር ሰፈራቸው አጥቃቸው” ወይም “በእነርሱ ላይ ድል አድራጊ እንድትሆን ስለማደርግ ምድያማውያንን በጦር ሰፈራቸው አጥቃቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ለመውረድ ፈራ

የታወቀውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “ወርዶ ለማጥቃት ፈራ”

ፉራ

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ድፍረትህ ይጨምራል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የምትሰማው ያበረታሃል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ኬላ

ወታደሮች የጠላትን ሰራዊት ለመቆጣጠር የሚቆሙበት አካባቢ ዳርቻ

Judges 7:12

የአንበጣው ብዛት እንደ ደመና የሚሸፍን

እዚህ ጋ “ደመና” ማለት መንጋ ነው። ደራሲው ምን ያህል ወታደሮች እንደነበሩ አጽንዖት ለመስጠት የአንበጣ መንጋ በማለት ስለ ሰራዊቱ ይናገራል።

ግመሎቻቸው በባህር ዳርቻ ከሚገኝ አሸዋ በቁጥር ይበልጥ ነበር

ደራሲው በጣም ብዙ ግመሎች መኖራቸውን በአጽንዖት ሲገልጽ ግነትን ይጠቀማል። ( ግነትና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

ግመሎቻቸው ከቁጥር በላይ ነበሩ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ግመሎቻቸው ማንም ሊቆጥራቸው ከሚችለው በላይ ነበሩ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 7:13

ይህ ከጌዴዎን ሰይፍ በስተቀር ሌላ አይደለም

እዚህ ጋ “የጌዴዎን ሰይፍ” የሚያመለክተው አጥቂውን የጌዴዎንን ሰራዊት ነው። አ.ት፡ “በሕልምህ ያየኸው የገብስ እንጎቻ የጌዴዎን ሰራዊት መሆን አለበት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር በምድያም ላይ ድልን ሰጠው

ይህ ወደፊታዊ ሁነት እንደ አላፊ ሁነት ሆኖ ተነግሯል። ይህ በእርግጠኝነት የሚፈጸም ስለመሆኑ አጽንዖት ይሰጣል። አ.ት፡ “በእርግጥ እስራኤላውያን ምድያማውያንን እንዲያሸንፉ እግዚአብሔር ይረዳቸዋል”

Judges 7:15

ሦስት መቶ ሰዎች

“300 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 7:17

ለእግዚአብሔርና ለጌዴዎን!

በውስጠ ታዋቂነት “እንዋጋለን” ማለት ነው። አ.ት፡ “ለእግዚአብሔርና ለጌዴዎን እንዋጋለን!”

Judges 7:19

አንድ መቶ ሰዎች

“100 ሰዎች” (ቁጥሮችን ተመልከት)

ልክ በእኩለ ሌሊት ጅማሬ ላይ

የእኩለ ሌሊት ጅማሬ ከምሽቱ 4 ሰዓት ገደማ ይሆናል።

Judges 7:20

የእግዚአብሔርና የጌዴዎን ሰይፍ

እዚህ ጋ “ሰይፍ” የሚያመለክተው ውጊያቸውን ነው። አ.ት፡ “ለእግዚአብሔርና ለጌዴዎን እንዋጋለን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 7:22

ሦስት መቶ መለከቶች

“300 መለከቶች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር የእያንዳንዱን ምድያማዊ ሰይፍ በባልንጀራው ላይ እንዲሆን አደረገ

እዚህ ጋ “ሰይፍ” የሚያመለክተው ሰይፍ በመጠቀም ማጥቃታቸውን ነው። አ.ት፡ “እያንዳንዱ ምድያማዊ ሰው ባልንጀራው ከሆነው ወታደር ጋር እንዲዋጋ እግዚአብሔር አደረገ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቤት ሺጣ - ጽሬራ - አቤላሞሖላ - ጠባት

እነዚህ የመንደሮችና የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከንፍታሌም፣ አሴርና ምናሴ ሁሉ የእስራኤል ሰዎች ተጠርተው ወጡ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ጌዴዎን እስራኤላውያንን ከንፍታሌም፣ አሴርና ከምናሴ ነገድ ሁሉ ጠራ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 7:24

ቤት ባራ

ይህ የእነስተኛ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እስከ ቤት ባራና ዮርዳኖስ ወንዝ ያሉትን ውሃዎች ተቆጣጠሩ

“የዮርዳኖስን ወንዝ አካባቢ እስከ ቤት ባራ ደቡብ ድረስ ተቆጣጠሩ”

በሔሬብ ዐለት - በዜብ የወይን መጭመቂያ

እስራኤላውያን ሔሬብና ዜብን በዚያ ከገደሉ በኋላ አካባቢዎቹ እነዚህ ስሞች ተሰጥተዋቸው ነበር።

ሔሬብ - ዜብ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 8

1 የኤፍሬም ሰዎች ለጌዴዎን እንዲህ አሉት፣ “ይህ በእኛ ላይ ያደረግኸው ምንድር ነው? ምድያምን ለመዋጋት በሄድህ ጊዜ እኛን አልጠራኸንም?” ከእርሱም ጋር በኃይል ተጣሉ። 2 እርሱም እንዲህ አላቸው፣ “ከእናንተ ጋር ሲነጻጸር አሁን እኔ ያደረግት ምንድን ነው? ከኤፍሬም የወይን ቃርሚያ ይልቅ የአቢዔዝር ሙሉ የወይን መከር አይሻልምን? 3 እግዚአብሔር በምድያም መሪዎች በሔሬብና በዜብ ላይ ድልን ሰጥቶአችኋል! ከእናንተ ጋር ሲነጻጸር እኑ ምን ፈጸምሁ?” ይህን በተናገረ ጊዜ ቍጣቸው በረደ። 4 ጌዴዎን ከእርሱ ጋር ከነበሩት ከሦስቱ መቶ ሰዎች ጋር ወደ ዮርዳኖስ መጣና ተሻገረ፡፡ እጅግ በጣም ደክመው ነበር፣ ይሁን እንጂ ያሳድዱ ነበር። 5 እርሱም ለሱኮት ሰዎች እንዲህ አላቸው፣ “ደክመዋልና እባካችሁ ለተከተሉኝ ሰዎች እንጀራ ስጡአቸው፣ እኔም የምድያምን ነገሥታት ዛብሄልንና ስልማናን እያሳደድሁ ነው፡፡” 6 የሱኮትም መሪዎች እንዲህ አሉ፣ “ዛብሄልንና ስልማናን በጉልበትህ አሸነፍኃቸውን?” እኛ ለሠራዊትህ እንጀራ ለምን እንደምንሰጥ አናውቅም? 7 ጌዴዎንም እንዲህ አለ፣ “እግዚአብሔር በዛብሄልና በስልማና ላይ ድል በሰጠኝ ጊዜ፣ እኔ በምድረ በዳ እሾህና በኵርንችት ሥጋችሁን እቦጫጭቀዋለሁ፡፡” 8 ከዚያም ወደ ጵኒኤል ወጣና በተመሳሳይ መንገድ በዚያ ለሚገኙ ሰዎች ተናገራቸው፣ ነገር ግን የጵንኤልም ሰዎች የሱኮት ሰዎች እንደ መለሱ መለሱለት። 9 እርሱም የጵኒኤልን ሰዎች ደግሞ እንዲህ አላቸው፣ “በሰላም በተመለስሁ ጊዜ፣ ይህን ግንብ አፈርሰዋለሁ፡፡ 10 ዛብሄልና ስልማናም ከሠራዊቶቻቸው ጋር፣ ከምሥራቅም ሰዎች ሠራዊት ሁሉ የቀሩ 15, 000 ያህል ሰዎች በቀርቀር ነበሩ፡፡ በሰይፍ ለመዋጋት ስልጠና የወሰዱ መቶ ሀያ ሺህ ሰዎች ወድቀው ነበርና፡፡ 11 ጌዴዎንም ዘላኖች ባሉበት መንገድ በኖባህና በዮግብሃ አልፎ ወደ ጠላት ሰፈር ሄደ፡፡ እርሱም የጠላትን ሰራዊት አሸነፈ፣ ምክንያቱም እንዲህ ዓይነት አደጋ ይገጥመናል ብለው አላሰቡም ነበርና፡፡ 12 ዛብሄልና ስልማናም ሸሹ፣ ጌዴዎንም ባሳደዳቸው ጊዜ ሁለቱንም የምድያም ነገሥታት ዛብሄልንና ስልማናን ያዛቸው፣ ሠራዊታቸውንም ሁሉ ድንጋጤ ላይ ጣላቸው፡፡ 13 የኢዮአስ ልጅ ጌዴዎንም በሔሬስ ዳገት በኩል በማለፍ ከጦርነት ተመለሰ፡፡ 14 እርሱም ከሱኮት ሰዎች አንድ ወጣት ይዞ ጠየቀውና ከእርሱ ምክር ፈለገ፡፡ ወጣቱም የሱኮትን መሪዎችና ሽማግሌዎች ሰባ ሰባት ሰዎች እነማን እንደሆኑ ገለጸለት። 15 ጌዴዎንም ወደ ሱኮት ሰዎች መጣና እንዲህ አላቸው፣ “‘ዛብሄልንና ስልማናን በጉልበትህ አሸነፍኃቸውን? እኛ ለሠራዊትህ እንጀራ መስጠት እንዳለብን አናውቅም?’ ብላችሁ ያላገጣችሁብኝ ዛብሄልና ስልማና ተመልከቱአቸው፡፡” 16 ጌዴዎንም የከተማይቱን ሽማግሌዎች ያዛቸው፣ የሱኮትንም ሰዎች በምድረ በዳ እሾህና በኵርንችት ገረፋቸው፡፡ 17 የጵኒኤልንም ግንብ አፈረሰ፣ የዚያችን ከተማ ሰዎችን ገደለ፡፡ 18 ጌዴዎንም ለዛብሄልና ለስልማና እንዲህ አላቸው፣ “በታቦር የገደላችኋቸው ሰዎች ምን ዓይነት ሰዎች ነበሩ?” እነርሱም፣ “እንደ አንተ ያሉ ነበሩ፡፡ እያንዳንዳቸው የንጉሥ ልጅ ይመስላሉ” አሉት፡፡ 19 ጌዴዎንም “እነርሱ የእናቴ ልጆች ወንድሞቼ ነበሩ፡፡ በሕይወት እንዲኖሩ አድናችኋቸው ቢሆን ኖሮ፣ ሕያው እግዚአብሔርን፣ እኔ አልገድላችሁም ነበር” አለ፡፡ 20 ለበኵር ልጁ ለዬቴር እንዲህ አለው፣ “ተነሳና ግደላቸው!” ነገር ግን ወጣቱ ልጅ ስለፈራ ሰይፉን አልመዘዘም፣ ምክንያቱም ገና ወጣት ልጅ ነበረና፡፡ 21 የዚያን ጊዜ ዛብሄልና ስልማና እንዲህ አሉ፣ “አንተ ተነሳና ግደለን! የሰው ኃይሉ እንደ ሰውነቱ ነውና፡፡” ጌዴዎንም ተነሥቶ ዛብሄልንና ስልማናን ገደላቸው፡፡ በግመሎቻቸውም አንገት ላይ የነበሩትን ጌጦች ወሰደ፡፡ 22 የእስራኤልም ሰዎች ጌዴዎንን “አንተ ግዛን፣ አንተ፣ የአንተ ልጅና የልጅ ልጆችህ ግዙን፣ ምክንያቱም አንተ ከምድያም ብርታት አድነኸናልና፡፡” 23 ጌዴዎንም ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ “እኔ በእናንተ ላይ አልገዛም፣ ልጄም በእናንተ ላይ አይገዛም፣ እግዚአብሔር ይገዛችኋል አላቸው፡፡ 24 ጌዴዎን ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ “አንድ የምጠይቃችሁ ነገር አለኝ፡- እያንዳንዳችሁ ከምርኮአችሁ ጕትቻችሁን እንድትሰጡኝ እለምናችኋለሁ፡፡” (ምድያማውያን የወርቅ ጕትቻ ነበራቸው ምክንያቱም እነርሱ እስማኤላውያንም ነበሩና፡፡) 25 እነርሱም፣ “ለአንተ ልንሰጥህ ደስተኞች ነን” አሉት፡፡ እነርሱም ልብስ አነጠፉና ሁሉም ሰው የምርኮውን ጕትቻ በዚያ ላይ ጣለ፡፡ 26 እርሱ የጠየቀው የወርቅ ጕትቻ ክብደት 1, 700 ሰቅል ወርቅ ነበር፡፡ ይህም ምርኮ ከጌጣ ጌጦቹ ሌላ የአንገት ጌጥ፣ የምድያምም ነገሥታት ከሚለብሱት ሐምራዊ ልብስ፣ እንደዚሁም በግመሎቻቸውም አንገት ከነበሩት ጌጦች ሌላ ነበረ፡፡ 27 ጌዴዎንም ከጉትቻዎቹ ባገኘው ወርቅ ኤፉድ ሠራና በከተማው፣ በዖፍራ አኖረው፣ እስራኤልም ሁሉ እርሱን በማምለክ አመነዘረበት፡፡ ለጌዴዎንና በቤቱም ላሉት ወጥመድ ሆነባቸው፡፡ 28 ስለዚህም ምድያም በእስራኤል ሕዝብ ፊት ተዋረደ፣ ራሳቸውንም እንደገና አላነሡም፡፡ በጌዴዎንም ዘመን ምድሪቱ ለአርባ ዓመት ሰላም ሆነች። 29 የኢዮአስም ልጅ ይሩበኣል ሄደና በራሱ ቤት ተቀመጠ። 30 ጌዴዎንም ብዙ ሚስቶች ነበሩትና ሰባ ወንዶች ልጆች ነበሩት፡፡ 31 በሴኬም የነበረችው ቁባቱም ወንድ ልጅ ወለደችለት፣ ጌዴዎንም ስሙን አቤሜሌክ ብሎ ጠራው፡፡ 32 የኢዮአስ ልጅ ጌዴዎን በመልካም የሽምግልና ዕድሜ ሞተ፣ በአቢዔዝራውያን ጎሳ በሆነው በዖፍራ በነበረው በአባቱ በኢዮአስ መቃብር ተቀበረ፡፡ 33 ጌዴዎን ከሞተ በኋላ ብዙ ሳይቆይ እንዲህ ሆነ፣ የእስራኤል ሕዝብ እንደገና ተመለሱ፣ የበኣልን አማልክት በማምለክ አመነዘሩ፡፡ በኣልብሪትንም አምላካቸው አደረጉ፡፡ 34 የእስራኤልም ሕዝብ በተለያዩ አቅጣጫዎች ከነበሩት ከጠላቶቻቸው ኃይል ያዳናቸውን አምላካቸውን እግዚአብሔርን አላሰቡትም፡፡ 35 እነርሱም ለእስራኤል ስላደረገው በጎ ነገር አስበው ለይሩበኣል (የጌዴዎን ሌላኛው ስም ነው) ውለታ ለመመለስ ቃል ኪዳናቸውን አልጠበቁም፡፡



Judges 8:1

ይህ ያደረግህብን ምንድነው?

የኤፍሬም ነገድ ሰዎች በሰራዊቱ ውስጥ እነርሱን ባለማካተቱ በዚህ ምላሽ በማይፈልግ ጥያቄ ጌዴዎንን ሲወቅሱት ነበር። ይህ እንደ መግለጫ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “በአግባቡ አላየኸንም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

በምድያም ላይ

እዚህ ጋ “ምድያም” የሚወክለው የምድያማውያንን ሰራዊት ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በኃይል ተሟገቱት

“ከእርሱ ጋር በቁጣ ተከራከሩ” ወይም “ክፉኛ ወቀሱት”

Judges 8:2

ከእናንተ ጋር ሲነጻጸር እኔ አሁን ያደረግሁት ምንድነው?

ጌዴዎን ይህንን ጥያቄ የሚያቀርበው የኤፍሬምን ሰዎች ለማክበር ነው። አ.ት፡ “እናንተ ካደረጋችሁት ጋር ሲነጻጸር እኔ ያደረግሁት በጣም ጥቂት ነው” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ከአቢዔዝር ሙሉ የወይን ምርት የኤፍሬም የወይን ቃርሚያ የሚሻል አይደለምን?

ጌዴዎን በዚህ ምላሽ በማያስፈልገው ጥያቄ አማካይነት የኤፍሬምን ሰዎች ያበርዳቸው ነበር። አ.ት፡ “እኛ የአቢዔዝር ተወላጆች ከሰበሰብነው ምርት በሙሉ ያለ ምንም ጥርጥር እናንተ የኤፍሬም ሰዎች የለቀማችሁት ወይን የተሻለ ነው!” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ከአቢዔዝር ሙሉ የወይን ምርት የኤፍሬም ቃርሚያ የተሻለ አይደለምን?

የጌዴዎንና የሰራዊቱ ምድያማውያንን ማሸነፍ የወይን ምርት እንደመሰብሰብ ተቆጥሮ ተነግሯል። የኤፍሬም ሰዎች በጦርነቱ መጨረሻ ሔሬብና ዜብን መግደላቸው ከመከር በኋላ የወይን ቃርሚያን እንደ ለቀሙ ተቆጥሮ ተነግሮላቸዋል። አ.ት፡ “እኛ የአቢዔዝር ተወላጆች በመጀመሪያ ካደረግነው ይልቅ እናንተ የኤፍሬም ሰዎች በጦርነቱ መጨረሻ ላይ ያደረጋችሁት ይበልጥ ታላቅ ነው” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አቢዔዝር

ይህ ከጌዴዎን ቅድም አያቶች የአንዱ ስም ነው። ጌዴዎን ስሙን ያገኘው ከአቢዔዝር ተወላጆችና ከምድራቸው ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር እና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሔሬብና ዜብ

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 7፡25 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ከእናንተ ጋር ሲነጻጸር እኔ ያከናወንኩት ምንድነው?

ጌዴዎን ይህንን ጥያቄ የሚያቀርበው የኤፍሬምን ሰዎች ለማክበር ነው። ይህ እንደ መግለጫ ሊገለጽ ይችላል። አ.ት፡ “እኔ ካደረግሁት ይልቅ እናንተ ያደረጋችሁት ይበልጥ ታላቅ ነው” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

በረደ

“ቀነሰ”

Judges 8:4

ሦስት መቶው ሰዎች

“300 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ማሳደዳቸውን ቀጠሉ

“ማሳደድ” የሚለው ቃል የነገር ስም ሲሆን እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ጠላቶቻቸውን ማባረራቸውን ቀጠሉ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ዛብሄልና ስልማና

እነዚህ የወንዶች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:6

የዛብሄልና የስልማና እጆች አሁን በእጅህ ውስጥ አሉ?

መሪዎቹ ጥያቄ የሚያቀርቡት እስራኤላውያኑ ዛብሄልንና ስልማናን ገና ያለመማረካቸውን አጽንዖት ለመስጠት ነው። አ.ት፡ “እስካሁን ዛብሄልና ስልማናን አልማረክኻቸውም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

የዛብሄልና የስልማና እጆች

እዚህ ጋ “እጆች” የሚያመለክተው ሙሉ ሰውነትን ነው።

አሁን በእጅህ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ኃይልን ወይም መቆጣጠርን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለሰራዊትህ እንጀራ የምንሰጠው ለምንድነው?

መሪዎቹ የሚጠይቁት ለእስራኤላውያኑ እንጀራ የሚሰጡበት ምንም ምክንያት እንደሌለ አጽንዖት ለመስጠት ነው። አ.ት፡ “ለሰራዊትህ እንጀራ የምንሰጥበትን አንዳች ምክንያት አላገኘንም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ቆዳችሁን በበረሃ እሾህና አሜከላ እተለትለዋለሁ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በይበልጥ መብራራት ይችላል። አ.ት፡ “በበረሃ እሾህና አሜከላ ጅራፍ በመሥራት እገርፋችኋለሁ፣ እቆራርጣችኋለሁ”

እሾህና አሜከላ

ስል፣ በሐረግ ወይም ዛፍ ቅርንጫፍ ላይ ጫፉ የሾለና ሰውና እንስሳን ለመቁረጥ የሚችል

Judges 8:8

ከዚያ ወጥቶ ሄደ

እዚህ ጋ በውስጠ ታዋቂነት የሚገኘው “እርሱ” የሚያመለክተው ጌዴዎንን ነው። ጌዴዎን የሚወክለው ራሱንና የሚከተሉትን ወታደሮች ነው። አ.ት፡ “ያንን ስፍራ ተዉ” ወይም “ጌዴዎንና 300 ሰዎቹ ያንን ስፍራ ተዉ”

ጵንኤል

የቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በዚያ ላሉ ሰዎች በተመሳሳይ መንገድ ተናገሯቸው

በውስጠ ታዋቂነት ያለውን መረጃ ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “እዚያም በተመሳሳይ መንገድ ምግብ እንዲሰጡት ጠየቀ” ወይም “እርሱም ደግሞ ምግብ እንዲሰጡት ጠየቃቸው”

በሰላም በምመለስበት ጊዜ

ይህ ጠላቶቹን ስለማሸነፉ የሚያመለክት የትህትና አነጋገር ነው። አ.ት፡ “የምድያማውያንን ሰራዊት ሙሉ በሙሉ ካሸነፍኩኝ በኋላ”

ይህንን ግምብ አፈርሰዋለሁ

እዚህ ጋ “እኔ” ጌዴዎንን የሚያመለክት ሲሆን ራሱንና ሰራዊቱን ይወክላል። አ.ት፡ “እኔና የእኔ ሰዎች ይህንን ግምብ እናፈርሰዋለን”

Judges 8:10

አሁን

ይህ ቃል እዚህ ጋ ጥቅም ላይ የዋለው የታሪኩ መስመር ለአፍታ ቆም ማለቱን ለማመልከት ነው። እዚህ ጋ ተራኪው የታሪኩን አዲስ ክፍል መናገር ይጀምራል።

ዛብሄልና ስልማና

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 8፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ቀርቀር

ይህ የአንድ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አስራ አምስት ሺህ ሰዎች

“15,000 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ወደቁ

ይህ በጦርነት የሞቱትን ሰዎች በትህትና የማመላከት መንገድ ነው። አ.ት፡ “ተገድለው ነበር” ወይም “በጦርነት ሞተው ነበር”

120,000 ሰዎች

“አንድ መቶ ሃያ ሺህ ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሰይፍ ይመዙ የነበሩ ሰዎች

እዚህ ጋ ሰይፍ መምዘዝ የሚወክለው በጦርነት ውስጥ በሰይፍ መጠቀምን ነው። ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ይህ ሐረግ የሚያመለክተው በጦርነት ውስጥ በሰይፍ የሚጠቀሙ ወታደሮችን ነው። አ.ት፡ “ሰይፍ የታጠቁ ሰዎች” ወይም “በሰይፍ የሚዋጉ ሰዎች” ወይም 2) ይህ ሐረግ የትኛውንም ወታደር ያመለክታል። አ.ት፡ “ወታደሮች” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:11

ጌዴዎን ወጥቶ ሄደ

እዚህ ጋ “ጌዴዎን” የሚወክለው ራሱንና ወታደሮቹን ሁሉ ነው። አ.ት፡ “ጌዴዎንና ወታደሮቹ ወጥተው ሄዱ”

አሸነፈ

እዚህ ጋ በውስጠ ታዋቂነት ያለው “እርሱ” የሚያመለክተው ጌዴዎንን ራሱንና ወታደሮቹን ሁሉ ነው። አ.ት፡ “ጌዴዎንና ወታደሮቹ አሸነፉ”

ኖባህና ዮግብሃ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዛብሄልና ስልማና

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 8፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ድንጋጤ

አንድ ሰው ማሰብ እንዳይችል ወይም በአግባቡ እንዳይሠራ የሚያስደርገው ታላቅ ፍርሃት ወይም ጭንቀት

Judges 8:13

የሐሬስ መተላለፊያ

ይህ በሁለት ተራራዎች መካከል የሚያልፍ መንገድ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ጠየቀውጠየቀው

ጌዴዎን ታዳጊውን ወጣት የጠየቀው ጥያቄ በግልጽ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “በከተማው ውስጥ ያሉትን መሪዎች በሙሉ ስማቸውን እንዲነግረው ጠየቀው”

ሰባ ሰባት አለቆች

“77 አለቆች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:15

ዛብሄልና ስልማና

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 8፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

አስቀድመህ ዛብሄልንና ስልማናን ድል አድርገሃቸዋል?

ጌዴዎን የሱኮት ሰዎች ሊሳለቁበት የጠየቁትን አባባል ይጠቅሳል። አ.ት፡ “ዛብሄልንና ስልማናን ገና ድል አላደረግሃቸውም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ጌዴዎን ወሰደ - ገረፋቸው - አፈረሰው

እዚህ ጋ “ጌዴዎን” የሚወክለው ራሱንና ወታደሮቹን ነው። አ.ት፡ “ጌዴዎንና ወታደሮቹ ወሰዱ - ገረፏቸው - አፈረሱት

እሾኽና አሜከላ

ስል፣ በሐረግ ወይም ዛፍ ቅርንጫፍ ላይ የሚገኝ፣ ጫፉ የሾለና ሰውና እንስሳን ለመቁረጥ የሚችል። ይህንን በመሳፍንት 8፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ጵንኤል

የከተማይቱን ስም በመሳፍንት 8፡8 ላይ በተረጎምከው መልኩ ተርጉመው።

Judges 8:18

ዛብሄልና ስልማና

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 8፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ታቦር

የዚህችን ከተማ ስም በመሳፍንት 4፡6 ላይ በተረጎምክበት መልክ ተርጉመው

አንተኑ የሚመስሉ ነበሩ

“ልክ አንተን ይመስሉ ነበር”

ሕያው እግዚአብሔርን

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሀይማኖታዊ መሓላ ሲሆን የሚናገረው እውነት መሆኑን አጽንዖት ለመስጠት ጥቅም ላይ ውሏል። አ.ት፡ “ቃል እገባላችኋለሁ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:20

ዮቴር

ይህ የጌዴዎን ልጅ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የሰው ኃይሉ እንደ ሰውነቱ ነው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “አንድ ሰው ሊያደርገው የሚገባው ሥራው ነው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ግማሽ ክብ

ይህ ሁለት ጫፍ ያለው ግማሽ ክብ ቅርጽ ነው። አብዛኛውን ጊዜ ይህ ቅርጽ የሚሆነው ጨረቃ በጥላ ስትጋረድ ነው።

ጌጣ ጌጦች

ማስዋቢያዎች

Judges 8:22

አንተ፣ ልጅህና የልጅ ልጅህ

ይህ የሚያሳየው እርሱ ከሞተ በኋላ የጌዴዎን ተወላጆች እንዲገዟቸው ነው። አ.ት፡ “አንተና አንተ ከሞትክ በኋላም ተወላጆችህ”

ከምድያም እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው በእስራኤል ላይ የሆነውን የምድያም ኃይል ነው። አ.ት፡ “ከምድያም ኃይል” ወይም “ከምድያም” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የምድያም

እዚህ ጋ “ምድያም” የሚወክለው የምድያምን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “ከምድያማውያን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:24

ጌዴዎን … አላቸው

“ጌዴዎን ለእስራኤል ሰዎች አላቸው”

ጉትቻዎች

በጆሮ ላይ የሚደረግ ጌጥ

ዘረፋ

በማስገደድ የተቀሙ ወይም በጦርነት ከተገደሉ ሰዎች የተወሰዱ ነገሮች

ምድያማውያን እስማኤላውያን ስለነበሩ የወርቅ ጉትቻዎች ነበሯቸው

እዚህ ጋ ተራኪው ስለ ምድያማውያን ዳራዊ መረጃ ይናገራል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ካባ

ረዘም ካለ ክር የሚሠራና እንደ ኮት በትከሻ ላይ የሚለበስ ልብስ

Judges 8:26

1,700 ሰቅል ወርቅ

“አንድ ሺህ ሰባት መቶ ሰቅል ወርቅ”። ዘመናዊውን የመጠን መለኪያ መጠቀም የሚያስፈልግ ከሆነ ይህንን ማድረግ የሚያስችሉ ሁለት መንገዶች አሉ። አ.ት፡ “18.7 ኪ.ግ ወርቅ” ወይም “ወደ 20 ኪ.ግ የሚጠጋ ወርቅ” (ቁጥሮች እና የመጽሐፍ ቅዱስ ክብደት መለኪያ የሚሉትን ተመልከት)

ግማሽ ክብ ቅርጽ ያላቸው ጌጣ ጌጦች

ይህንን በመሳፍንት 8፡21 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

በአንገት ጌጥ ላይ የሚንጠለጠሉ ድሪዎች

በአንገት ሀብል ወይም ክር ላይ የሚንጠለጠሉ ትናንሽ ጌጣጌጦች

የምድያም ነገሥታት ይለብሱት የነበረውን

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የምድያም ነገሥታት የለበሱት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:27

ጌዴዎን በጉትቻዎቹ ኤፉድ ሠራ

“ጌዴዎን የወርቅ ጉትቻዎቹን ኤፉድ ለመስሪያነት ተጠቀመበት”

ዖፍራ

የከተማይቱን ስም በመሳፍንት 6፡11 እንዳደረግኸው ተርጉመው።

በዚያ እስራኤል ሁሉ አመነዘሩበት

ይህ አመንዝራነትን በሚመስል መልክ ሐሰተኛ አምላክን ስለ ማምለካቸው ይናገራል። አ.ት፡ “እስራኤላውያን በዚያ ኤፉዱን በማምለካቸው በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአትን ሠሩ” ( ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እስራኤል በሙሉ

እዚህ ጋ “በሙሉ” በጣም ብዙዎቹ ልብሱን ማምለካቸውን አጽንዖት ለመስጠት የተደረገ ግነት ነው። አ.ት፡ “በእስራኤል በጣም ብዙ ሰዎች ልብሱን አመለኩት” (ግነትና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

እርሱም ለጌዴዎንና በቤቱ ላሉት ወጥመድ ሆነባቸው

ይህ አደን የሚያድን ሰው የሚያጠምደው ወጥመድ ይመስል ጌዴዎንና ቤተሰቡ ኤፉዱን ሊያመልኩት እንደተፈተኑ ያሳያል። አ.ት፡ “ለጌዴዎንና ለቤተሰቡ ፈተና ሆነባቸው” ወይም “ጌዴዎንና ቤተሰቡ እርሱን በማምለክ ኃጢአትን ሠሩ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በቤቱ ላሉት

እዚህ ጋ “በቤቱ” የሚወክለው የጌዴዎንን ቤተሰብ ነው። አ.ት፡ “ለቤተሰቡ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ስለዚህ ምድያም ለእስራኤል ሕዝብ ተገዛላቸው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሰለዚህ እግዚአብሔር ምድያማውያን በእስራኤል ሕዝብ ፊት እንዲገዙ አደረጋቸው” ወይም “ስለዚህ እስራኤላውያን ምድያማውያንን እንዲያሸንፉ እረዳቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ራሳቸውን ቀና አላደረጉም

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንደገና እስራኤልን አላጠቁም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ስለዚህ ምድሪቱ ዐርፋ ነበር

እዚህ ጋ “ምድሪቱ” የሚወክለው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “ስለዚህ እስራኤላውያን በሰላም ኖሩ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አርባ ዓመት

x

Judges 8:29

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ስሙን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሰባ ወንዶች ልጆች

“70 ወንዶች ልጆች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:32

ረጅም ዕድሜ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “በጣም በሸመገለ ጊዜ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ተቀበረ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ቀበሩት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ዖፍራ

የዚህችን ከተማ ስም በመሳፍንት 6፡11 እንዳደረግኸው ተርጉመው።

ከአቢዔዝር ጎሳ

የዚህን የሕዝብ ወገን ስም በመሳፍንት 6፡11 እንዳደረግኸው ተርጉመው።

እንዲህም ሆነ

ይህ ሐረግ ጥቅም ላይ የዋለው የታሪኩ አዲስ ክፍል መጀመሩን ለማመልከት ነው። በቋንቋህ ይህንን ማድረግ የሚያስችል መንገድ ካለ ልትጠቀምበት ትችላለህ።

እንደገና ተመለሱ

ሕዝቡ እግዚአብሔርን መተዋቸው በአካል ከእርሱ እንደተለዩ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን ማምለካቸውን አቆሙ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በኣልን በማምለክ አመነዘሩ

ሐሰተኛ አማልክትን ማምለካቸው እንደ አመንዝራነት ተቆጥሮ ተነግሯል። አ.ት፡ “በኣልን በማምለክ በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአትን ሠሩ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በኣልብሪት

ይህ የሐሰተኛ አምላክ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 8:34

ከጠላቶቻቸው እጅ ሁሉ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ኃይልን ወይም መቆጣጠርን ነው። አ.ት፡ “ከጠላቶቻቸው ኃይል ሁሉ” ወይም “ከጠላቶቻቸው ሁሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በየአቅጣጫው

“የከበቧቸውን “

የይሩበአል ቤት

እዚህ ጋ “የ…ቤት” የሚወክለው የአንድን ሰው ቤተሰብ ነው። አ.ት፡ “የይሩበአል ቤተሰብ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ይህንን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።


Chapter 9

1 የይሩበኣል ልጅ አቤሜሌክ ወደ እናቱ ዘመዶች ወደ ሴኬም ሄደና ለእነርሱና ለእናቱ ቤተሰብ ጎሳ በሙሉ እንዲህ አላቸው፣ 2 “በሴኬም የሚገኙ መሪዎች በሙሉ ይሰሙ ዘንድ ይህን ተናገሩ፣ ‘ለእናንተ የሚሻለው የትኛው ነው? የይሩበኣል ሰባ ልጆች ሁሉ ቢገዙአችሁ ወይስ አንድ ሰው ቢገዛችሁ?’ እኔ የአጥንታችሁ ፍላጭ የሥጋችሁ ቍራጭ እንደ ሆንሁ አስቡ፡፡” 3 የእናቱም ዘመዶች ስለ እርሱ ለሴኬም መሪዎች ተናገሩ፣ እነርሱም አቤሜሌክን ለመከተል ተስማሙ፣ “እርሱ ወንድማችን ነው” ብለዋልና፡፡ 4 እነርሱም ከበኣልብሪትም ቤት ሰባ ብር ሰጡት፣ አቤሜሌክም እርሱን የተከተሉትን ስርዓት አልበኞችንና ወሮበሎችን ለመቅጠር ተጠቀበመት፡፡ 5 እርሱም ወደ አባቱ ቤት ወደ ዖፍራ ሄደ፣ የይሩበኣልን ልጆች ሰባ ወንድሞቹን በአንድ ድንጋይ ላይ አረዳቸው፡፡ ትንሹ የይሩበኣል ልጅ ኢዮአታም ግን ተሸሽጎ ስለነበር እርሱ ብቻ ተረፈ፡፡ 6 የሴኬምና የቤትሚሎ መሪዎች ሁሉ በአንድ ላይ ተሰበሰቡ፣ እነርሱም ሄደው በሴኬም በዓምዱ አጠገብ ባለው በበሉጥ ዛፍ ስር አቤሜሌክን አነገሡት፡፡ 7 ለኢዮአታም ይህን ነገር በነገሩት ጊዜ፣ በገሪዛን ተራራ ራስ ላይ ሄደና ቆመ፡፡ ድምፁንም ከፍ አድርጎ ጮኸና እንዲህ አላቸው፣ “እናንተ የሴኬም መሪዎች፣ እግዚአብሔርም እናንተን ይሰማ ዘንድ፣ እኔን ስሙኝ፡፡ 8 አንድ ጊዜ ዛፎች በእነርሱ ላይ የሚያነግሱት ለመቀባት ሄዱ፡፡ እነርሱም ለወይራ ዛፍ ‘በእኛ ላይ ንገሥ’ አሉት፡፡ 9 የወይራ ዛፍ ግን ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ ‘እግዚአብሔርና ሰዎችን ለማክበር የሚጠቅመውን ቅባቴን ትቼ ተመልሼ በሌሎች ዛፎች ላይ ለመወዛወዝ ልሂድን?’ 10 ዛፎቹም ለበለስ ዛፍ እንዲህ አሉት፣ ‘መጥተህ በእኛ ላይ ንገሥ፡፡’ 11 ነገር ግን የበለሱ ዛፍ፣ ጣፋጭነቴንና መልካሙን ፍሬዬን ትቼ ተመልሼ በሌሎች ዛፎች ላይ ለመወዛወዝ ልሂድን?’ አላቸው፡፡ 12 ዛፎችም ለወይኑ፣ ‘መጥተህ በእኛ ላይ ንገሥ’ አሉት፡፡ 13 ወይኑም፣ እግዚአብሔርንና ሰውን ደስ የሚያሰኘውን አዲስ የወይን ጠጄን ትቼ ተመልሼ በዛፎች ላይ ለመወዛወዝ ልሂድን? አላቸው፡፡ 14 ከዚያም ዛፎች ሁሉ የእሾህ ቁጥቋጦን፣ ‘መጥተህ በእኛ ላይ ንገሥ’ አሉት፡፡ 15 የእሾህ ቁጥቋጦውም ዛፎቹን፣ ‘በእውነት እኔን በእናንተ ላይ እንድነግስ ልትቀቡኝ የምትፈልጉ ከሆነ፣ ኑና በጥላዬ ስር ተጠለሉ፡፡ እንዲህ ካልሆነ ግን እሳት ከእሾህ ቁጥቋጦ ይውጣና የሊባኖስንም ዝግባ ያቃጥል’ አላቸው፡፡ 16 አሁን እንግዲህ፣ አቤሜሌክን ባነገሳችሁት ጊዜ በእውነትና በቅንነት አድርጋችሁ ከሆነ፣ ለይሩበኣልና ለቤቱም በጎነት አስባችሁ አድርጋችሁ ከሆነ፣ እንዳደረገውም መጠን ለእርሱ የተገባውን ቀጥታችሁት ከሆነ 17 አባቴ ስለ እናንተ ተዋግቶ እንደነበር፣ ሕይወቱን አሳልፎ በመስጠት፣ ከምድያምም እጅ እናንተን እንዳዳናችሁ አሰባችሁ ማለት ነው 18 ነገር ግን ዛሬ እናንተ በአባቴ ቤት ላይ ተነሥታችኋል፣ በአንድ ድንጋይ ላይ ልጆቹን፣ ሰባ ሰዎችን፣ አረዳችኋቸው፡፡ ከዚያም የሴት አገልጋዩን ልጅ አቤሜሌክን ዘመዳችሁ ስለ ሆነ በሴኬም መሪዎች ላይ እንዲነግስ አደረጋችሁት፡፡ 19 ያንጊዜ ለይሩበኣልና ለቤቱ በእውነትና በቅንነትን አድርጋችሁ ከሆነ፣ እንግዲያው እናንተ በአቤሜሌክ ደስ ሊላችሁ ይገባል፣ እርሱም በእናንተ ደስ ይበለው፡፡ 20 ነገር ግን እንዲህ ባይሆን፣ ከአቤሜሌክ እሳት ይውጣና የሴኬምንም ሰዎችና የቤትሚሎን ቤት ያቃጥል፡፡ ከሴኬምም ሰዎችና ከቤትሚሎ እሳት ይውጣና አቤሜሌክን ያቃጥል፡፡ 21 ኢዮአታምም ሸሽቶ አመለጠ፣ ከዚያም ወደ ብኤር ሄደ፡፡ እርሱም በዚያ ተቀመጠ ምክንያቱም ከአቤሜሌክ ከወንድሙ በጣም ሩቅ ነበረ፡፡ 22 አቤሜሌክም በእስራኤል ላይ ለሦስት ዓመት ገዛ፡፡ 23 እግዚአብሔር በአቤሜሌክና በሴኬም መሪዎች መካከል ክፉን መንፈስ ሰደደ፡፡ የሴኬም መሪዎችም በአቤሜሌክ ላይ የነበራቸውን እምነት ጥለው ከዱት፡፡ 24 እግዚአብሔር ይህንን ያደረገው በሰባዎቹ የይሩበኣል ልጆች ላይ የተደረገውን ዓመፅ ለመበቀል ነው፣ ወንድማቸው አቤሜሌክም እነርሱን በመግደሉ ተጠያቂ እንዲሆን ለማድረግ ነው፤ የሴኬም ሰዎችም እርሱ ወንድሞቹን እንዲገድላቸው ስለተባበሩት ተጠያቂ እንዲሆኑ ለማድረግ ነው፡፡ 25 ስለዚህ የሴኬም መሪዎች በኮረብቶች ራስ ላይ እርሱን አድፍጠው የሚጠብቁ ሰዎች መደቡ፣ እነርሱም በዚያ መንገድ በአጠገባቸው ያለፉትን ሰዎች በሙሉ ዘረፉ፡፡ ይህም ወሬ ለአቤሜሌክ ደረሰው፡፡ 26 የአቤድም ልጅ ገዓል ከዘመዶቹ ጋር መጣና ወደ ሴኬም ሄዱ፡፡ የሴኬም መሪዎች በእርሱ ተማመኑበት፡፡ 27 እነርሱም ወደ እርሻው ወጥተው ሄዱና ከወይን አትክልት ቦታ ወይን ለቅመው ጨመቁት፡፡ በአምላካቸው ቤት የደስታ በዓል አደረጉ፣ በሉም ጠጡም፣ አቤሜሌክንም ሰደቡ፡፡ 28 የአቤድም ልጅ ገዓል እንዲህ አለ፣ “እናገለግለው ዘንድ አቤሜሌክ ማን ነው? ሴኬምስ ማን ነው? እርሱ የይሩብኣል ልጅ አይደለምን? ዜቡልስ የእርሱ ሹም አይደለምን? ለኤሞር ሰዎች፣ ለሴኬም አባት አገልግሉ! ለምን እርሱን እናገለግላለን? 29 ይህ ሕዝብ በእኔ አዛዥነት ስር ቢሆን እመኝ ነበር! የዚያን ጊዜ አቤሜሌክን አስወግደው ነበር፡፡ ለአቤሜሌክም ‘ሠራዊትህን ሁሉ ጥራ’ እለው ነበር፡፡” 30 የከተማይቱ ሹም፣ ዜቡል የአቤድን ልጅ የገዓልን ቃል በሰማ ጊዜ ቁጣው ነደደ፡፡ 31 ወደ አቤሜሌክም ያታልለው ዘንድ እንዲህ ብሎ መልክተኞች ላከ፣ “ተመልከት፣ የአቤድ ልጅ ገዓልና ዘመዶቹ ወደ ሴኬም እየመጡ ነው፣ ከተማይቱን በአንተ ላይ እንድትሸፍት አነሳስተዋል፡፡ 32 አሁንም አንተና ከአንተ ጋር ያሉት ወታደሮች በሌሊት ተነሡ፣ ሜዳውም ላይ አድፍጡ፡፡ 33 ከዚያም በጠዋት ፀሐይ በወጣች ጊዜ ማልደህ ተነሣና በከተማይቱ ላይ ድንገተኛ ጥቃት ፈጽምባት፡፡ እርሱና ከእርሱ ጋር ያሉት ሕዝብ በአንተ ላይ በመጡ ጊዜ በእነርሱ ላይ ልታደርግ የምትችለውን ማንኛውንም ነገር አድርግባቸው፡፡” 34 ስለዚህ አቤሜሌክ በሌሊት ተነሳ፣ እርሱና ከእርሱ ጋር የነበሩት ሰዎች በሙሉ፣ በአራት ወገን ተከፋፍለው በሴኬም ላይ አደፈጡ፡፡ 35 የአቤድ ልጅ ገዓል ወጥቶ በከተማይቱ በር መግቢያ ቆመ፡፡ አቤሜሌክና ከእርሱ ጋር የነበሩት ሰዎችም ከተደበቁበት ስፍራ ወጥተው መጡ፡፡ 36 ገዓልም ሰዎቹን ባየ ጊዜ ዜቡልን፣ “ተመልከት፣ ሰዎች ከኮረብቶች ራስ ወርደው እየመጡ ነው!” አለው፡፡ ዜቡልም እንዲህ አለው፣ “አንተ የምታየው ሰዎች የሚመስለውን የኮረብቶች ጥላ ነው፡፡” 37 ገዓልም እንደገና እንዲህ ሲል ተናገረ፣ “ተመልከት፣ በምድር መካከል ሰዎች ወርደው እየመጡ ነው፣ አንድም ወገን በቃላተኞች የበሉጥ ዛፍ መንገድ እየመጣ ነው፡፡ 38 የዚያን ጊዜ ዜቡል እንዲህ አለው፣ “‘እናገለግለው ዘንድ አቤሜሌክ ማን ነው?’ ብለህ የተናገርሃቸው እነዚያ የትዕቢት ቃላቶችህ አሁን የት አሉ? እነዚህ ሰዎች አንተ የናቅሃቸው አይደሉምን? አሁን ውጣና ከእነርሱ ጋር ተዋጋ፡፡” 39 ገዓል ወጣና የሴኬም ሰዎችን ይመራ ነበር፣ ከአቤሜሌክም ጋር ተዋጋ፡፡ 40 አቤሜሌክም አሳደደው፣ ገዓልም በፊቱ ሸሸ፡፡ ብዙዎቹም በከተማይቱ በር መግቢያ ፊት ለፊት በከባድ ሁኔታ ቆስለው ወደቁ፡፡ 41 አቤሜሌክም በአሩማ ተቀመጠ፡፡ ዜቡልም ገዓልንና ዘመዶቹን ከሴኬም እንዲወጡ አስገደዳቸው፡፡ 42 በሚቀጥለው ቀን የሴኬም ሕዝብ ወደ እርሻ ሄዱ፣ ይህም ወሬ ለአቤሜሌክ ደረሰው፡፡ 43 ሕዝቡንም ወሰደ፣ በሦስት ወገንም ከፈላቸውና በእርሻዎቹ ውስጥ አደፈጡ፡፡ እርሱም ተመለከተ፣ ሕዝቡ ከከተማ ወጥተው ሲመጡ አየ፡፡ እርሱም ተዋጋቸውና ገደላቸው፡፡ 44 አቤሜሌክና ከእርሱም ጋር የነበሩት ወገኖች ተዋጉና የከተማይቱን በር መግቢያ ዘጉ፡፡ ሌሎቹ ሁለት ወገኖች ደግሞ በእርሻው ውስጥ የነበሩትን ሁሉ ወጓቸውና ገደሉአቸው፡፡ 45 አቤሜሌክም ቀኑን ሙሉ ከከተማይቱ ጋር ተዋጋ፡፡ ከተማይቱንም ተቆጣጠረና በውስጧ የነበሩትን ሕዝብ ገደላቸው፡፡ የከተማይቱንም ቅጥር አፈራረሰው፣ በላይዋም ጨው በተነባት፡፡ 46 የሴኬም ግንብ መሪዎች በሙሉ ይህንን ወሬ በሰሙ ጊዜ፣ ወደ ኤልብሪት ቤት ምሽግ ውስጥ ገቡ፡፡ 47 አቤሜሌክም መሪዎቹ በሙሉ በሴኬም ግንብ ውስጥ በአንድ ላይ እንደተሰበሰቡ ተነገረው፡፡ 48 አቤሜሌክ ወደ ሰልሞን ተራራ ወጣ፣ እርሱና ከእርሱ ጋር የነበሩት ሰዎች ሁሉ፡፡አቤሜሌክም በእጁ መጥረቢያ ወሰደና የዛፉን ቅርንጫፎች ቆረጠ፡፡ እርሱም አንሥቶ በትከሻው ላይ አደረገውና ከእርሱ ጋር የነበሩትን ሰዎች እንዲህ ብሎ አዘዛቸው፣ “እኔ ሳደርግ ያያችሁትን፣ ፈጥናችሁ እኔ እንዳደረግሁ አድርጉ፡፡” 49 ስለዚህ እያንዳንዱ ሰው የዛፉን ቅርንጫፎች ቈረጠና አቤሜሌክን ተከተሉት፡፡ እነርሱም ቅርንጫፎቹን በምሽጉ ላይ ከመሩአቸው፣ በላዩም ላይ እሳት አቀጣጠሉበት፣ ከዚህ የተነሳ የሴኬም ግንብ ሰዎች ሁሉ፣ አንድ ሺህ የሚያህሉ ወንድና ሴት ሞቱ፡፡ 50 ከዚያ በኋላ አቤሜሌክ ወደ ቴቤስ ሄደ፣ ቴቤስንም ከበባትና ተቆጣጠራት፡፡ 51 ነገር ግን በከተማይቱ ጠንካራ ግንብ ነበረ፣ የከተማይቱም ሰዎች ሁሉ፣ ወንዶችና ሴቶች ሁሉ፣ የከተማይቱም መሪዎች ሁሉ ወደዚያ ሸሹና በውስጥ ሆነው ደጁን ዘጉት፡፡ ከዚያም እስከ ግንቡ ሰገነት ድረስ ወደ ላይ ወጡ፡፡ 52 አቤሜሌክም ወደ ግንቡ መጣና ተዋጋ፣ በእሳትም ሊያቃጥለው ወደ ግንቡ በር አጠገብ መጣ፡፡ 53 ነገር ግን አንዲት ሴት በአቤሜሌክ ራስ ላይ የወፍጮ መጅ ጣለችበት፣ መጁም ጭንቅላቱን ሰባበረው፡፡ 54 ከዚያም እርሱ በአስቸኳይ ጋሻ ጃግሬውን ጠርቶ፣ “አንድም ሰው እኔን ‘ሴት ገደለችው’ እንዳይል ሰይፍህን መዝዘህ ግደለኝ” አለው፡፡ ስለዚህ ወጣቱ ሰው ወጋውና ሞተ፡፡ 55 የእስራኤልም ሰዎች አቤሜሌክ እንደ ሞተ ባዩ ጊዜ ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡ 56 እግዚአብሔርም ሰባ ወንድሞቹን በመግደል አቤሜሌክ በአባቱ ላይ ያደረገውን ክፋት ተበቀለው፡፡ 57 እግዚአብሔርም የሴኬምን ሰዎች ክፋት ሁሉ በራሳቸው ላይ መለሰባቸው፣ የይሩበኣልም ልጅ የኢዮአታም እርግማን በእነርሱ ላይ መጣባቸው፡፡



Judges 9:1

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ይህንን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

እባካችሁ፣ በሴኬም ያሉ መሪዎች ሁሉ እንዲሰሙ እንዲህ በሉ፣ ‘ሰባዎቹ የይሩበዓል ልጆች ቢገዟችሁ ወይስ አንዱ ብቻ ቢገዛችሁ ይሻላችኋል?’

ይህ በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ ያለ ትዕምርተ ጥቅስ ነው። ቀጥተኛው ትዕምርተ ጥቅስ ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ሆኖ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እባካችሁ፣ የይሩበዓል ሰባ ልጆች ሁሉ እንዲገዟቸው ይፈልጉ እንደሆን ወይም ከልጆቹ አንዱ ብቻ እንዲገዛቸው ይፈልጉ እንደሆን የሴኬምን መሪዎች ጠይቋቸው” (በትዕምርተ ጥቅስ ውስጥ የሚገኝ ትዕምርተ ጥቅስ እና ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ የሚለውን ተመልከት)

ሰባ

“70” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

እኔ አጥንታችሁና ሥጋችሁ ነኝ

እዚህ ጋ “አጥንታችሁና ሥጋችሁ” የሚወክለው የአንድ ሰው ዘመድ መሆንን ነው። አ.ት፡ “እኔ የቤተሰባችሁ አባል ነኝ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:3

የእናቱ ዘመዶች ስለ እርሱ ለመሪዎቹ ነገሯቸው

ይህ ማለት የአቤሜሌክ የእናቱ ዘመዶች አቤሜሌክን ንጉሣቸው እንዲያደርጉት አሳብ በማቅረብ ለመሪዎቹ ተናገሩ።

አቤሜሌክን ለመከተል ተስማሙ

“አቤሜሌክ መሪያቸው እንዲሆን ተስማሙ”

ቤቱ

እዚህ ጋ “ቤት” የሚወክለው መቅደስን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰባ ጥሬ ብር

ይህ ማለት ሰባ ሰቅል ብር ነው። አንድ ሰቅል 11 ግራም ይመዝናል። ይህንን ወደ ዘመናዊ መለኪያ መተርጎም አስፈላጊ ከሆነ እንደዚህ አድርገህ ልትተረጉመው ትችላለህ። አ.ት፡ “አንድ ኪሎ የሚያህል ጥሬ ብር” (ገንዘብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚለውን ተመልከት)

ሰባ

“70” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በኣልብሪት

ይህ የሐሰተኛ አምላክ ስም ነው። እርሱን በመሳፍንት 8፡33 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሕገ ወጦችንና ግድ የለሾችን

“ቁጡና ሞኞች”

Judges 9:5

ዖፍራ

በመሳፍንት 6፡11 ላይ እንዳደረግኸው የዚህችን ከተማ ስም ተርጉመው።

አንድ ድንጋይ

“1 ድንጋይ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሰባ

“70” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ይህንን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ቤት ሚሎ

ይህ የቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:7

ለኢዮአታም ይህ በተነገረው ጊዜ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አቤሜሌክ ወንድሞቹን መግደሉን ኢዮአታም በሰማ ጊዜ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ገሪዛን ተራራ

ይህ ተራራ ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዛፎች በላያቸው ላይ ንጉሥ ለማንገሥ ተሰበሰቡ። የወይራውን ዛፍ ‘በእኛ ላይ ንገሥ’ አሉት

ኢዮአታም ሰዎች የሚያደርጓቸውን ነገሮች በዛፎች በመመሰል ያብራራል። (ምሳሌዎች እና ሰውኛ የሚሉትን ተመልከት)

በላያቸው ላይ ንጉሥ ለመቀባት

እዚህ ጋ በዘይት መቀባት አንድን ሰው ንጉሥ እንዲሆን መሾምን የሚወክል ምሳሌአዊ ድርጊት ነው። አ.ት፡ “በሁላቸውም ላይ እንዲገዛ ንጉሥ ለመሾም”

በእኛ ላይ ንገሥ

“ንጉሣችን ሁን”

Judges 9:9

የወይራው ዛፍ እንዲህ አላቸው - የበለስ ዛፍ እንዲህ አላቸው

ኢዮአታም ሰዎች የሚያደርጓቸውን ነገሮች በዛፎች ምሳሌ አድርጎ ያብራራል። (ምሳሌዎች እና ሰውኛ የሚሉትን ተመልከት)

በሌሎች ዛፎች ላይ - ዘይት መስጠቴን መተው አለብኝ?

የወይራው ዛፍ ንጉሥ መሆንን እምቢ ለማለት ይህንን ጥያቄ ይጠይቃል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “በሌሎች ዛፎች ላይ … ዘይት መስጠቴን አላቆምም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

መወዛወዝ

“መወዛወዝ” ማለት በንፋስ ምክንያት ወደ ፊትና ወደ ኋላ ማለት ነው። ዛፉ ይህንን ሐረግ የሚጠቀመው “መግዛት” ለማለት ነው።

በሌሎች ዛፎች ላይ - ጣፋጭነቴን መተው አለብኝ?

የበለስ ዛፉ ንጉሥ መሆንን እምቢ ለማለት ይህንን ጥያቄ ይጠይቃል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “በሌሎች ዛፎች ላይ … ጣፋጭነቴን አላቆምም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ጣፋጭነቴንና መልካሙን ፍሬዬን

“ጣፋጭነት” የሚለው ቃል የነገር ስም ነው። በዛፉ ላይ የሚበቅለውን ፍሬ ለመግለጽ እንደ ቅጽል ሆኖ ሊነገር ይችላል። (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:12

ዛፎቹ የወይንን ተክል እንዲህ አሉት

በዚህ ምሳሌ ኢዮአታም ሰዎች የሚያደርጓቸውን ነገሮች ዛፎቹና የወይን ተክል እንደሚያደርጉት አድርጎ ያብራራል። (ምሳሌዎች እና ሰውኛ የሚሉትን ተመልከት)

በሌሎች ዛፎች ላይ -- አዲሱን ወይኔን ማቆም አለብኝ?

የወይን ተክሉ ንጉሥ መሆንን እምቢ ለማለት ይህንን ጥያቄ ይጠይቃል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “በሌሎች ዛፎች ላይ … አዲሱን ወይኔን አላቆምም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

የእሾህ ቁጥቋጦ

እሾህ የሚጎዳ የሾለ መውጊያ አለው። ይህ ቁጥቋጦ በየቅርንጫፎቹ ላይ በርካታ ሹል መውጊያዎች አሉት።

Judges 9:15

የእሾህ ቁጥቋጦው ለዛፎቹ እንዲህ አላቸው

በዚህ ምሳሌ ኢዮአታም የቁጥቋጦው እሾህና ዛፎቹ ሰዎች የሚያደርጓቸውን ነገሮች እንደሚያደርጉ ያብራራል። (ምሳሌዎች እና ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

በላያችሁ እንድነግሥ ልትቀቡኝ

አንድን ሰው በዘይት መቀባት ንጉሥ እንዲሆን የመሾም ምሳሌአዊ ድርጊት ነው። አ.ት፡ “ንጉሣችሁ አድርጋችሁ ልትቀቡኝ” (ምሳሌአዊ ድርጊት የሚለውን ተመልከት)

ደህንነት እንዲሆንላችሁ

“ደህንነት” የሚለው ቃል የነገር ስም ሲሆን እንደ ቅጽል ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ተጠበቁ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

እሳት ከእሾህ ቁጥቋጦው ይውጣ፣ የሊባኖስንም ዝግባዎች ያቃጥል

ይህ ማለት ዝግባዎቹን ለማቃጠል የእሾህ ቁጥቋጦው ይነዳል።

ከዚያም እሳት ከእሾህ ቁጥቋጦው ይውጣ

የእሾህ ቁጥቋጦው ራሱን እንደ “እሾህ ቁጥቋጦ” ያመለክታል። አ.ት፡ “ከዚያም እሳት ከእኔው ከእሾህ ቁጥቋጦው ይውጣ” (አንደኛ፣ ሁለተኛ ወይም ሦስተኛ መደብ የሚለውን ተመልከት)

አሁን

ይህ “በዚህ ሰዓት” ማለት አይደለም፣ ነገር ግን ትኩረትን ወደሚቀጥለው አስፈላጊ ጉዳይ ለመሳብ ጥቅም ላይ ውሏል።

ለይሩበአልና ለቤቱ መልካም አድርጋችሁ ከሆነና የሚገባውን ቅጣት ሰጥታችሁት ከሆነ

ኢዮአታም ያደረጉት መልካም ይሆን እንደሆነ ምርጫውን ያቀርብላቸዋል፤ ይሁን እንጂ ያደረጉት በመሠረቱ መልካም እንደሆነ ኢዮአታም አያምንም። አ.ት፡ “መልካም የሆነውን አድርጋችሁ ከሆነና ልጆቹን ሁሉ ትገድሉበት ዘንድ ለይሩበአል የሚገባው ከሆነ”

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ይህንን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተምልከት።

ቤቱ

እዚህ ጋ “ቤት” የጌዴዎንን ቤተሰብ ይወክላል። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:17

ከምድያማውያን እጅ -- አባቴ እንደተዋጋላችሁ ለማሰብ

እዚህ ጋ ጌዴዎን የሴኬምን ሰዎች ለማዳን ከተዋጋ በኋላ የሴኬም ሰዎች ለጌዴዎንና ለቤተሰቡ በክፋት መመለሳቸውን ኢዮአታም ማመን እንደማይችል ይገልጻል።

ከምድያማውያን እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ኃይልን ወይም መቆጣጠርን ነው። አ.ት፡ “ከምድያማውያን ኃይል” ወይም “ከምድያማውያን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ተነሣችሁበት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ተቃወማችሁ” ወይም “በእርሱ ላይ አምጻችኋል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የአባቴ ቤት

እዚህ ጋ “ቤት” የሚወክለው ቤተሰብን ነው። አ.ት፡ “የአባቴ ቤተሰብ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰባ

“70” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አንድ ድንጋይ

“1 ድንጋይ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሴት ባሪያው

እዚህ ጋ “የእርሱ” የሚያመለክተው ጌዴዎንን ነው።

Judges 9:19

ከጌዴዎንና ከቤቱ ጋር በታማኝነትና በቅንነት አድርጋችሁ ከሆነ

ኢዮአታም ያደረጉት መልካም ይሆን እንደሆነ ምርጫውን ያቀርብላቸዋል፣ ይሁን እንጂ ያደረጉት በመሠረቱ መልካም እንደሆነ ኢዮአታም አያምንም። አ.ት፡ “ለይሩበአልና ለቤተሰቡ ሊደረግላቸው የሚገባቸውን አድርጋችሁላቸው ከሆነ”

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። እንዲህ ማለትም፣ “በኣል ለራሱ ይሟገት” ማለት ነው። ይህንን በ6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ለቤቱ

እዚህ ጋ “ቤት” የሚያመለክተው ቤተሰብን ነው። አ.ት፡ “ቤተሰቡን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ካልሆነ ግን

ኢዮአታም ያደረጉት ክፉ መሆኑን እና እርግማን እንደሚሆንባቸው ተቃራኒውን አማራጭ ያቀርብላቸዋል። ኢዮአታም ያደረጉት ክፉ መሆኑን ያምናል። አ.ት፡ “ለይሩበአልና ለቤተሰቡ ሊደረግ የማይገባቸውን አድርጋችሁ ከሆነ ግን”

ከአቤሜሌክ እሳት ይውጣ፣ የሴኬምንም ሰዎች ያንድድ

ኢዮአታም የሚናገረው እርግማንን ነው። አቤሜሌክ በእሳት ያቃጥላቸው ይመስል የሴኬምን ሰዎች እንደሚያጠፋቸው ይናገራል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አቤሜሌክን ለማንደድ እሳት ከሴኬምና ከቤትሚሎ ሰዎች ይውጣ

ኢዮአታም የሚናገረው እርግማንን ነው። የሴኬምና የቤትሚሎ ሰዎች በእሳት ያቃጥሉት ይመስል አቤሜሌክን እንደሚያጠፉት ይናገራል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቤትሚሎ

ይህ የቦታ ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 9፡6 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ብኤር

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:22

እግዚአብሔር በአቤሜሌክና በሴኬም መሪዎች መካከል ክፉ መንፈስን ላከ

ይህ ማለት ኢዮአታም በአቤሜሌክና በሴኬም መሪዎች መካከል አለመግባባትንና ጠላትነትን እንዲፈጥር ክፉ መንፈስን በመላክ ያደረገውን እርግማን እግዚአብሔር ተግባራዊ አድርጎታል ማለት ነው።

ወንድሞቹን እንዲገድል ስለረዱት -- ስላደረጉት ግፍ እግዚአብሔር ይህንን አደረገ

ተደራጊ ድምፅ ያላቸውን ሐረጎች በአድራጊ ድምፅ መናገር ይቻላል። አ.ት፡ “አቤሜሌክ ስለገደላቸው ሰባ ልጆችና የሴኬም ሰዎች በግድያው ስለረዱት እግዚአብሔር ለመበቀል ይህንን አደረገ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሰባ

“70” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ይህንን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Judges 9:25

አደጋ እንዲጥሉበት በኮረብታማው ስፍራ ሰዎች አድፍጠው እንዲጠብቁት አደረጉ

“ሰዎች በኮረብታው ጫፍ እንዲደበቁና አቤሜሌክን ለመግደል እንዲጠባበቁ ላካቸው”

ይህ ለአቤሜሌክ ተነገረው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሰዎች ሊያጠቁት እየተጠባበቁ እንዳሉ አንድ ሰው ለአቤሜሌክ ነገረው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:26

ገዓል -- አቤድ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ተማምነውበት ነበር

“መተማመን” የሚለው ቃል የነገር ስም ሲሆን “መታመን” በሚል ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ታመኑበት” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ወደ ሜዳ ወጡ

እዚህ ጋ “እነርሱ” የሚያመለክተው ገዓልን፣ ዘመዶቹንና የሴኬምን ሰዎች ነው።

ረገጣቸው

ይህንን ያደረጉት የወይን ጭማቂ ለማዘጋጀት ነው።

ረገጡ

“ሰባበሩ” ወይም “ጨፈለቁ”

በቤቱ ውስጥ

እዚህ ጋ “ቤት” የሚወክለው መቅደስን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:28

ገዓል -- ኤቤድ

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 9፡26 ላይ እንዴት እንደተርጎምከው ተመልከት።

እንድናገለግለው አቤሜሌክ ማነው? ሴኬምስ ማነው?

ገዓል የሰኬም ሰዎች አቤሜሌክን ማገልገል እንደሌለባቸው አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ይጠይቃል። አ.ት፡ “አቤሜሌክን ማገልገል የለብንም!” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

እንድናገለግለው አቤሜሌክ ማነው? ሴኬምስ ማነው?

እነዚህ ሁለቱም ጥያቄዎች አንድ ናቸው። የአቤሜሌክ እናት ከሴኬም በመሆኗ ምክንያት ገዓል አቤሜሌክን ለማመልከት “ሴኬም” ይላል። አ.ት፡ “አቤሜሌክን ማገልገል የለብንም፣ እርሱም ሴኬም ነው!” ( እና ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ የይሩበአል ልጅ አይደለምን? ዜቡልስ የእርሱ ሹም አይደለምን?

ገዓል የሰኬም ሰዎች አቤሜሌክን ማገልገል እንደሌለባቸው አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ይጠይቃል። አ.ት፡ “እርሱ የይሩበአል ልጅ ብቻ ነው፣ ዜቡልም የእርሱ ሹም ብቻ ነው” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ይህንን በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ዜቡል

ይህ የሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የሴኬምን አባት የኤሞርን ሰዎች አገልግሉ

ገዓል የሚለው፣ የሴኬም ሰዎች ማገልገል ያለባቸው እውነተኛ ከነዓናውያን የሆኑትን ከኤሞር የተወለዱትን እንጂ እስራኤላዊ አባት ያለውን ሰው ማገልገል የለባቸውም።

አቤሜሌክን የምናገለግለው ለምንድነው?

ገዓል የሰኬም ሰዎች አቤሜሌክን ማገልገል እንደሌለባቸው አጽንዖት ለመስጠት ጥያቄ ይጠይቃል። አ.ት፡ “አቤሜሌክን ማገልገል የለብንም!” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

እነዚህ ሰዎች ከትዕዛዜ ስር እንዲሆኑ እመኛለሁ

“የሴኬምን ሰዎች ባስተዳድር እመኛለሁ”

Judges 9:30

ዜቡል

ይህንን ስም በመሳፍንት 9፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

የኤቤድን ልጅ የገዓልን ቃል ሰሙ

“የኤቤድ ልጅ ገዓል የተናገረውን ሰሙ”

ገዓል -- ኤቤድ

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 9፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

ቁጣው ነደደ

መቆጣቱ እንደ እሳት መንደድ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “በጣም ተቆጣ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለማታለል

ዜቡል ገዓልንና የሴኬምን ሰዎች እያታለላቸው ነው። አ.ት፡ “በምስጢር”

ከተማይቱን በአንተ ላይ እያነሣሡ ነው

ይህ የከተማው ሰዎች በድስት ውስጥ እንዳለ ፈሳሽ መንተክተካቸውን ያሳያል። አ.ት፡ “የከተማይቱ ሰዎች በአንተ ላይ እንዲያምጹ እያነሣሧቸው ነው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከተማይቱ

እዚህ ጋ “ከተማ” የሚወክለው በከተማይቱ የሚኖሩትን ሰዎች ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:32

አሁን

ይህ “በዚህ ሰዓት” ማለት አይደለም፣ ነገር ግን ትኩረትን ወደሚቀጥለው አስፈላጊ ጉዳይ ለመሳብ ጥቅም ላይ ውሏል።

ደፈጣ

“ተደብቆ እነርሱን በድንገት ማጥቃት”

የምትችለውን አድርግባቸው

ይህ ማለት የገዓልን ተከታዮች ለማጥፋት የፈለጉትን ማድረግ ይችላሉ።

Judges 9:34

ከእርሱ ጋር የነበሩት ሰዎች ሁሉ

“አቤሜሌክን የተከተሉ ሰዎች ሁሉ” ወይም “ለአቤሜሌክ ይዋጉ የነበሩ ሰዎች ሁሉ”

በሴኬም ላይ የሚያደፍጡትን አስቀመጡ

እዚህ ጋ “ሴኬም” የሚወክለው የሴኬምን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “የሴኬምን ሰዎች በድንገት ለማጥቃት ተደበቁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አራት ቦታ አካፍሎ

“በ4 ቡድኖች ለያይቶ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ገዓል -- ኤቤድ

እነዚህን ስሞች በመሳፍንት 9፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

Judges 9:36

ገዓል

ይህ የሰው ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 9፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ዜቡል

ይህ የሰው ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 9፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የምትመለከተው ሰዎችን የሚመስሉ የኮረብቶችን ጥላ ነው

ዜቡል ገዓልን እያደናገረውና ለጦርነት እንዳይዘጋጅ እያዘገየው ነው። አ.ት፡ “ያ ሰዎች ሳይሆኑ በኮረብቶቹ ላይ ጥላዎች ብቻ ናቸው”

አንድ ክፍል

“1 ቡድን” ወይም “1 ጓድ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:38

ዜቡል

በመሳፍንት 9፡28 ላይ ይህንን ስም እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

አሁን የትዕቢት ቃልህ የት አለ?

ዜቡል በዚህ ምላሽ በማይፈልግ ጥያቄ በገዓል ላይ እየተሳለቀበት ነው። አ.ት፡ “አሁን በትዕቢት አትናገርም” ወይም “አሁን አትታበይም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

‘እናገለግለው ዘንድ አቤሜሌክ ማነው?’ ያልከው አንተ

ዜቡል የገዓልን የኩራት ንግግር መልሶ እየጠቀሰለት ነው። ይህ እንደ መግለጫና ቀጥተኛ እንዳልሆነ ትዕምርተ ጥቅስ ተደርጎ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “አቤሜሌክን ማገልገል የለብንም ብለህ የነበርከው አንተ” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ እና ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆኑ ትዕምርተ ጥቅሶች የሚለውን ተመልከት)

እነዚህ አንተ የናቅኻቸው ሰዎች አይደሉምን?

ዜቡል በዚህ ምላሽ በማይፈልግ ጥያቄ ገዓልን እየተገዳደረው ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “የናቅኻቸው ሰዎች እኝውልህ” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

የተናቁ

እጅግ ያልተወደዱ ወይም የተጠሉ

ገዓል

ይህንን ስም በመሳፍንት 9፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ብዙዎች ክፉኛ ቆስለው ወደቁ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ብዙ ሰዎች ቆስለው ሞቱ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:41

አሩማ

ይህ የአንድ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዜቡል

ይህ የሰው ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 9፡28 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ገዓል

ይህ የሰው ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 9፡26 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ይህ ለአቤሜሌክ ተነገረው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ይህንን ለአቤሜሌክ ነገረው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በሦስት ክፍል ከፋፈላቸው

“በ3 ቡድኖች ለያያቸው” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በእርሻው ውስጥ የሚያደፍጡትን አኖሩ

x

Judges 9:44

ቡድኖቹ

“የወታደሮቹ ቡድኖች”

ሌሎች ሁለት

“ሌሎች 2” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አቤሜሌክ ተዋጋ -- አጠፋ

እዚህ ጋ “አቤሜሌክ” የሚወክለው ራሱንና ወታደሮቹን ነው። አ.ት፡ “አቤሜሌክና ወታደሮቹ ተዋጉ … አጠፉ”

በከተማይቱ ላይ

እዚህ ጋ “ከተማ” የሚወክለው ሰዎችን ነው። አ.ት፡ “በሴኬም ሰዎች ላይ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አጠፉ

“አወደሙ”

ጨው ዘራባት

“በምድሪቱ ላይ ጨው ዘራ”። በምድር ላይ ጨው መዝራት በዚያ ቦታ ምንም ነገር እንዳይበቅል ያደርጋል።

Judges 9:46

ቤቱ

እዚህ ጋ ይህ የሚወክለው መቅደስን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ኤልበሪት

“ኤል” የሚለው ቃል ትርጉም “አምላክ” ማለት ነው። ይህ በመሳፍንት 8፡33 እንዳለው “በኣል በሪት” ሁሉ ያው ሐሰተኛ አምላክ ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ለአቤሜሌክ ተነገረው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ለአቤሜሌክ ነገረው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:48

ሰልሞን ተራራ

ይህ የተራራ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ቆለለ

ይህ ማለት ቅርንጫፎቹን በብዙ መጠን እንደ ክምር መከመር ነው።

አንድ ሺህ የሚያህሉ ሰዎች

“1,000 ያህል ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 9:50

ቴመስ

ይህ የአንድ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ቴመስን ከበበ

“ከቴመስ ከተማ ውጪ ሰፈረ”

Judges 9:52

ተዋጋት

“አጠቃት”

የወፍጮ መጅ

ሁለት ትላልቅና ጠፍጣፋ ድንጋዮች ጥራጥሬ ለመፍጨት ያገለግሉ ነበር። በታችኛው ላይ በመንከባለል በመሐል ያለውን ጥራጥሬ የሚፈጨው ከላይ የሚሆነው መጅ ነው።

ጋሻ ጃግሬ

ይህ የአቤሜሌክን የጦር መሣሪያ የሚሸከመው ሰው ነው።

ወጋው

ይህ ማለት ወጣቱ አቤሜሌክን በሰይፍ ወጋው።

Judges 9:55

ሰባ

“70” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የሴኬምን ሰዎች ክፋት ሁሉ በራሳቸው ላይ መለሰባቸው

እዚህ ጋ “ክፋት በራሳቸው ላይ ተመለሰ” የሚለው የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ስላደረጉት ክፋት ሁሉ የሴኬምን ሰዎች ቀጣቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የይሩበአል ልጅ የኢዮአታም እርግማን ደረሰባቸው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “የይሩበአል ልጅ የኢዮአታም እርግማን መጣባቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ይሩበአል

ይህ የጌዴዎን ሌላው ስሙ ነው። ይህንን ስም በመሳፍንት 6፡32 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።


Chapter 10

1 ከአቤሜሌክ በኋላ ከይሳኮር ነገድ የሆነውና በኮረብታማውም በኤፍሬም አገር ባለችው በሳምር ይኖር የነበረው የዱዲ ልጅ የፎሖ ልጅ ቶላ እስራኤልን ለማዳን ተነሣ፡፡ 2 እርሱም በእስራኤል ላይ ሀያ ሦስት ዓመት ፈረደ፡፡ እርሱም ሞተ፣ በሳምርም ተቀበረ፡፡ 3 ከእርሱም በኋላ ገለዓዳዊው ኢያዕር ተነሣ፡፡ በእስራኤልም ላይ ሀያ ሁለት ዓመት ፈረደ፡፡ 4 በሠላሳ አህያዎች የሚጋልቡ ሠላሳ ልጆች ነበሩት፣ እነርሱም በገለዓድ ምድር ያሉ እስከ ዛሬ ድረስ የኢያዕር መንደሮች ተብለው የሚጠሩ ሠላሳ ከተሞች ነበሩአቸው፡፡ 5 ኢያዕርም ሞተ፣ በቃሞንም ተቀበረ፡፡ 6 የእስራኤል ሕዝብ ከዚህ በፊት ከሰሩት በላይ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ስራ ጨምረው ሠሩ፣ በኣልን፣ አስታሮትን፣ እንደዚሁም የሶርያን አማልክት፣ የሲዶናን አማልክት፣ የሞዓብን አማልክት፣ የአሞንን ሕዝብ አማልክት፣ የፍልስጥኤማውያንን አማልክት አመለኩ፡፡እግዚአብሔርን ተዉ፣ እርሱንም አላመለኩትም፡፡ 7 የእግዚአብሔርም ቍጣ በእስራኤል ላይ ነደደ፣ እርሱም ፍልስጥኤማውያንና አሞናውያን ያሸንፉአቸው ዘንድ ለእነርሱ አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ 8 እነርሱም በዚያን ዓመት የእስራኤልን ሕዝብ አደቀቋቸው፣ አስጨነቋቸው፣ ለአሥራ ስምንት ዓመት በዮርዳኖስ ማዶ በአሞራውያን ምድር በገለዓድ ውስጥ የነበሩትን የእስራኤልን ሕዝብ ሁሉ አስጨነቋቸው፡፡ 9 የአሞንም ሰዎች ከይሁዳ፣ ከብንያምና ከኤፍሬም ቤት ጋር ለመዋጋት ዮርዳኖስን ተሻገሩ፣ ከዚህ የተነሳ እስራኤል እጅግ በጣም ተጨነቁ፡፡ 10 የዚያን ጊዜ የእስራኤልም ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር ጮሁ፣ እንዲህ በማለት፣ “በአንተ ላይ በድለናል፣ ምክንያቱም አምላካችንን ትተን የበኣል አማልክትን አምልከናልና፡፡” 11 እግዚአብሔርም ለእስራኤል ልጆች እንዲህ አላቸው፣ “ከግብፃውያን፣ ከአሞራውያንም፣ ከአሞናውያን፣ ከፍልስጤማውያንና 12 ከሲዶናውያን አላዳንኋችሁምን? አማሌቃውያንና ማዖናውያን አስጨነቋችሁ፤ ወደ እኔም ጮኻችሁ፣ እኔም ከእነርሱ ኃይል አዳንኋችሁ፡፡ 13 ይሁን እንጂ እናንተ እንደገና ተዋችሁኝና ሌሎችን አማልክት አመለካችሁ፡፡ ስለዚህ፣ እኔም ከእንግዲህ ወዲህ አላድናችሁም፡፡ 14 ሂዱና ወደምታመልኳቸው አማልክት ጩኹ፡፡ በመከራችሁ ጊዜ እነርሱ ያድኑአችሁ፡፡ 15 የእስራኤልም ሕዝብ እግዚአብሔርን እንዲህ አሉት፣ “እኛ ኃጢአትን ሠርተናል፡፡ ለአንተ ደስ የሚያሰኝህን ማንኛውንም ነገር በእኛ ላይ አድርግብን፡፡ እባክህ፣ የዛሬን ብቻ አድነን፡፡” 16 እነርሱም በመካከላቸው ካሉት ባዕዳን አማልክት ዘወር አሉ፣ እግዚአብሔርንም አመለኩ፡፡እርሱም የእስራኤልን ጕስቍልና ሊታገሰው የማይቻለው ሆነ፡፡ 17 ከዚያም አሞናውያን በአንድ ላይ ተሰበሰቡና በገለዓድ ሰፈሩ፡፡ እስራኤላውያንም በአንድ ላይ ተሰበሰቡና ሰፈራቸውን በምጽጳ ላይ አደረጉ፡፡ 18 የገለዓድ ሕዝብ መሪዎችም እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ፣ “አሞናውያንን ለመዋጋት የሚጀምር ሰው ማን ነው? እርሱ በገለዓድ በሚኖሩ ሰዎች ሁሉ ላይ መሪ ይሆናል፡፡”



Judges 10:1

ቶላ -- ፎሐ -- ዱዲ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሳምር

ይህ የቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እስራኤልን ለማዳን ተነሣ

“እስራኤልን ለማዳን መጣ” ወይም “እስራኤልን ለማዳን መሪ ሆነ”

እስራኤልን ለማዳን

እዚህ ጋ “እስራኤል” የሚወክለው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእስራኤል ላይ ፈረደ

እዚህ ጋ “ፈረደ” ማለት የእስራኤልን ሕዝብ መራ ማለት ነው።

ሃያ ሦስት ዓመት

“23 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ተቀበረ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ቀበሩት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 10:3

ከእርሱ ቀጥሎ ገለዓዳዊው ኢያዕር

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከቶላ በኋላ ገለዓዳዊው ኢያዕር መሪ ነበር” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ኢያዕር

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ገለዓዳዊው

ኢያዕር ከገለዓድ ነገድ ነበር

በእስራኤል ላይ ፈረደ

እዚህ ጋ “ፈረደ” ማለት የእስራኤልን ሕዝብ መራ ማለት ነው።

እስራኤል

እዚህ ጋ “እስራኤል” የሚወክለው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሃያ ሁለት ዓመት

“22 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሠላሳ ወንዶች ልጆች

“30 ወንዶች ልጆች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሐቮዝጃኤር

ይህ በአንድ ሰው ስም የሚጠራ የአውራጃ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እስካሁን ድረስ

ይህ ማለት መጽሐፈ መሳፍንት እስከሚጻፍበት ጊዜ ድረስ ማለት ነው።

ተቀበረ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ቀበሩት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ቃሞን

ይህ የቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 10:6

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ማድረጋቸውን አበዙ

አንድ ሰው እየጨመረበት እንደሚያተልቀው አንዳች ነገር ይህ የተነገረው ስለ ክፋት ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ክፉ ነው ያለውን ማድረጋቸውን ቀጠሉ”። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእግዚአብሔር ፊት

የእግዚአብሔር ፊት የሚወክለው የእርሱን ፍርድ ወይም ምዘና ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔር እንደሚለው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አስታሮቶች

ይህ የአስታሮት ብዙ ቁጥር ሲሆን በተለያየ ቅርጽ የምትመለክ እንስት አምላክ ነበረች። ይህንን በመሳፍንት 2፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

እግዚአብሔርን ተዉት፣ አላመለኩትምም

በመሠረቱ ደራሲው ሁለት ጊዜ የተናገረው ስለ አንድ ነገር አጽንዖት ለመስጠት ነው። እነዚህ ሊጣመሩ የሚችሉ ናቸው። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን ማምለካቸውን ሙሉ በሙሉ አቆሙ”

እግዚአብሔርን ተዉት

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔርን አለማምለካቸውና አለመታዘዛቸው ሰዎቹ እግዚአብሔርን ትተው ወደ አንድ የሆነ ቦታ እንደሄዱ ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእስራኤል ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ነደደ

ቁጣ የሚነድ እሳት ይመስል እግዚአብሔር እንደ ተቆጣ ተነግሯል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር በእስራኤል ላይ በጣም ተቆጣ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በፍልስጥኤማውያንና በአሞናውያን እጅ ሸጣቸው

እግዚአብሔር ፍልስጥኤማያንና አሞናውያን እስራኤላውያንን እንዲያሸንፉ መፍቀዱ እስራኤላውያንን ለእነርሱ እንደሸጠላቸው ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በ… እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው ኃይልን ወይም መቆጣጠርን ነው። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 10:8

አደቀቋቸውና አስጨነቋቸው

እነዚህ ሁለት ቃላት የሚሉት በመሠረቱ ስለ አንድ ነገር ሲሆን እስራኤላውያን ምን ያህል እንደተሰቃዩ አጽንዖት ለመስጠት ነው። አ.ት፡ “በከፋ ሁኔታ አስጨነቋቸው”

አሥራ ስምንት ዓመት

“18 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ከዮርዳኖስ ማዶ የነበሩት

ይህ ማለት ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምስራቅ ማለት ነው።

በገለዓድ ያለው

“ይህ አውራጃም ደግሞ ገለዓድ ተብሎ ተጠርቷል”

ይሁዳ - ብንያም

“ይሁዳ” እና “ብንያም” የእነዚያን ነገዶች ሕዝቦች ያመለክታል። አ.ት፡ “የይሁዳ ነገድ ሕዝቦች … የብንያም ነገድ ሕዝቦች”። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የኤፍሬም ቤት

እዚህ ጋ “ቤት” የሚያመለክተው የኤፍሬምን ነገድ ሕዝቦች ነው። አ.ት፡ “የኤፍሬም ነገድ ሕዝቦች”። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በመሆኑም እስራኤል እጅግ ተጨነቀ

“እስራኤል” የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “በመሆኑም የእስራኤል ሕዝብ በጣም ተሰቃየ”። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 10:10

የእስራኤል ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ

ይህ ማለት የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሔር እንዲረዳቸው በፍጹም ልባቸው ጠየቁት።

አምላካችንን በመተዋችን ምክንያት

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔርን አለማምለካቸውና አለመታዘዛቸው ሰዎቹ እግዚአብሔርን ትተው ወደ አንድ የሆነ ቦታ እንደሄዱ ሆኖ ተነግሯል። ( ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አምላካችንን ትተነዋል

ሕዝቡ የሚናገሩት ስለ እግዚአብሔር ሲሆን “አምላካችን” ብለው ይጠሩታል። ይህ በሁለተኛ መደብ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አምላካችን ሆይ፣ አንተን ትተንሃል” (አንደኛ፣ ሁለተኛ፣ ወይም ሦስተኛ መደብ የሚለውን ተመልከት)

ሲዶናውያን -- አላዳንኋችሁምን?

ሌሎች አማልክትን ስለማምለካቸው እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ይገስጻቸዋል። ይህ መልስ የማይሻ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከሲዶናውያን … ያዳንኋችሁ እኔ ነኝ” (መልስ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ማዖናውያን

እነዚህ ከማዖን ቤተሰብ ወይም ጎሳ የሆኑ ሕዝቦች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከኃይላቸው

እዚህ ጋ “ኃይል” የሚወክለው አማሌቃውያንን እና ማዖናውያንን ነው። አ.ት፡ “ከእነርሱ”። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 10:13

እንደ ገና ተዋችሁኝ

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔርን አለማምለካቸውና አለመታዘዛቸው ሰዎቹ እግዚአብሔርን ትተው ወደ አንድ የሆነ ቦታ እንደሄዱ ሆኖ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእንግዲህ ወዲህ አላድናችሁም

“ከእንግዲህ ወዲህ” የሚለው ሐረግ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ትርጉሙም አንድ ነገር በማድረግ መቀጠል ማለት ነው። በእግዚአብሔር አነጋገር ውስጥ ግልጽ ያልሆነውን ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “በተደጋጋሚ እናንተን ማዳኔን አልቀጥልም” ወይም “እናንተን ማዳን ማቆሜን እርግጠኛ መሆን ትችላላችሁ”

Judges 10:15

በመካከላቸው ያሉትን እንግዶች አማልክት

የዚህን መግለጫ ግልጽ ያልሆነ ትርጉም ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “የወረሷቸውን የእንግዶች አማልክት ምስሎች”

እግዚአብሔር የእስራኤልን ስቃይ ለመታገስ አልቻለም

እዚህ ጋ እስራኤል የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል ሕዝብ ከእንግዲህ ወዲያ እንዲሰቃይ አልፈለገም”።(ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 10:17

ከአሞናውያን ጋር በመዋጋት የሚጀምርልን ሰው ማነው?

“አሞናውያንን ለመዋጋት ሰራዊታችንን የሚመራው ማን ነው?”


Chapter 11

1 ገለዓዳዊውም ዮፍታሔ ኃያል ተዋጊ ነበር፣ ነገር ግን የጋለሞታ ሴት ልጅ ነበረ፡፡ አባቱም ገለዓድ ነበረ፡፡ 2 የገለዓድም ሚስት ደግሞ ሌሎች ወንዶች ልጆችን ወለደችለት፡፡ የሚስቱ ልጆች ባደጉ ጊዜ፣ ዮፍታሔን ቤቱን ለቅቆ እንዲወጣ አስገደዱት፣ እንዲህም አሉት፡- “አንተ ከቤተሰባችን ምንም ነገር አትወርስም፡፡ አንተ የሌላ ሴት ልጅ ነህ፡፡” 3 ስለዚህ ዮፍታሔ ከወንድሞቹ ፊት ሸሸና በጦብ ምድር ተቀመጠ፡፡ ስርዓት አልበኛ ሰዎችም ተከተሉት፣ ተሰብስበውም ከእርሱ ጋር ሄዱ፡፡ 4 ከጥቂት ቀናት በኋላ፣ የአሞን ሰዎች ከእስራኤል ጋር ውጊያ አደረጉ፡፡ 5 የአሞንም ሰዎች ከእስራኤል ጋር ውጊያ ባደረጉ ጊዜ፣ የገለዓድ ሽማግሌዎች ዮፍታሔን ከጦብ ምድር ለማምጣት ሄዱ፡፡ 6 ዮፍታሔንም፣ “ና፣ ከአሞን ሰዎች ጋር እንድንዋጋ አለቃችን ሁን” አሉት፡፡ 7 ዮፍታሔም ለገለዓድ ሽማግሌዎች እንዲህ አላቸው፣ “እናንተ ጠልታችሁኛል፣ የአባቴንም ቤት ትቼ እንድሄድ አስገድዳችሁኛል፡፡ አሁን በተቸገራችሁ ጊዜ ለምን ወደ እኔ መጣችሁ?” 8 የገለዓድም ሽማግሌዎችም ለዮፍታሔ፣ “አሁን ወደ አንተ የተመለስነው ለዚህ ነው፤ ከእኛ ጋር ና፣ ከአሞንም ሰዎች ጋር ተዋጋ፣ ከዚያም በኋላ በገለዓድ በሚኖሩት ሰዎች ሁሉ ላይ መሪ ትሆናለህ” አሉት፡፡ 9 ዮፍታሔም ለገለዓድ ሽማግሌዎች፣ “ከአሞን ሰዎች ጋር እንድዋጋ እንደገና ወደ ቤቴ ከመለሳችሁኝ፣ እግዚአብሔርም በእነርሱ ላይ ድል ከሰጠን መሪያችሁ እሆናለሁ” አላቸው፡፡ 10 የገለዓድ ሽማግሌዎችም ለዮፍታሔ፣ “እንደተናገርነው የማናደርግ ከሆነ እግዚአብሔር በእኛ መካከል ምስክር ይሁን” አሉት፡፡ 11 ስለዚህ ዮፍታሔ ከገለዓድ ሽማግሌዎች ጋር ሄደ፣ ሕዝቡም በላያቸው ላይ መሪና የጦር አዛዥ አደረጉት፡፡ እርሱ በምጽጳ በእግዚአብሔር ፊት በነበረ ጊዜ፣ ዮፍታሔ የገባውን ቃል ኪዳን ሁሉ ደገመው፡፡ 12 ዮፍታሔም ወደ አሞን ሰዎች ንጉሥ እንዲህ በማለት መልእክተኞችን ላከ፡- “በእኛ መካከል ያለው ጠብ ምንድን ነው? ምድራችንን ለመውሰድ በጦር ለምን መጣህ?” 13 የአሞንም ሰዎች ንጉሥም ለዮፍታሔ መልክተኞች “እስራኤል ከግብፅ በወጣ ጊዜ ከአርኖን ጀምሮ እስከ ያቦቅና እስከ ዮርዳኖስ ድረስ ምድሬን ወስደዋል፡፡ አሁን እነዚህን መሬቶች በሰላም መልሱልኝ” ብሎ መለሰላቸው፡፡ 14 ዮፍታሔም ወደ አሞን ሰዎች ንጉሥ መልክተኞችን እንደ ገና ላከ፣ 15 እንዲህም አለው፣ “ዮፍታሔ የሚለው ይህንን ነው፡- እስራኤል የሞዓብን ምድር የአሞንንም ሰዎች ምድር አልወሰደም፣ 16 ነገር ግን ከግብፅ በወጡ ጊዜ፣ እስራኤል በምድረ በዳ በኩል ወደ ቀይ ባሕር ከዚያም ወደ ቃዴስ ሄዱ፣ 17 እስራኤል ወደ ኤዶምያስ ንጉሥ እንዲህ በማለት መልእክተኞችን ላኩ፣ ‘በምድርህ እንድናልፍ እባክህ ፍቀድልን፣’ ነገር ግን የኤዶምያስ ንጉሥ አልሰማም፡፡ እንዲሁም ወደ ሞዓብ ንጉሥ መልእክተኞች ላኩ፣ እርሱም አልፈቀደም፡፡ ስለዚህ እስራኤል በቃዴስ ተቀመጠ፡፡ 18 እነርሱም በምድረ በዳ በኩል ሄዱና ከኤዶምያስና ከሞዓብ ምድር ተመለሱ፣ በሞዓብም ምድር በምሥራቅ በኩል ሄዱ፣ በአርኖንም ማዶ ሰፈሩ፡፡ ነገር ግን ወደ ሞዓብ ክልል ውስጥ አልገቡም፣ አርኖን የሞዓብ ድንበር ነበረና፡፡ 19 እስራኤልም በሐሴቦን ውስጥ ገዥ ወደነበረው ወደ አሞራውያን ንጉሥ ወደ ሴዎን መልክተኞችን ላከ፤ እስራኤልም ‘እባክህ፣ በምድርህ በኩል ወደ ስፍራችን እንድናልፍ ፍቀድልን’ አለው፡፡ 20 ነገር ግን ሴዎን እስራኤል በድንበሩ እንዲያልፍ አላመነውም፡፡ ስለዚህ ሴዎን ሰራዊቱን ሁሉ ሰበሰበና ወደ ያሀጽ ተንቀሳቀሰ፣ በዚያም ከእስራኤል ጋር ተዋጋ፡፡ 21 የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔርም ለእስራኤል በሴዎን ላይ ድል ሰጠውና ሕዝቡን ሁሉ በቁጥጥራቸው ስር እንዲሆኑ አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ስለዚህም እስራኤል በዚያች አገር ተቀምጠው የነበሩትን የአሞራውያንን አገር ሁሉ ወሰዱ፡፡ 22 በአሞራውያን ክልል ውስጥ የነበረውን ሁሉንም ነገር ወሰዱ፣ ከአርኖንም እስከ ያቦቅ ድረስ፣ ከምድረ በዳውም እስከ ዮርዳኖስ ድረስ፡፡ 23 ያንጊዜ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር አሞራውያንን ከሕዝቡ ከእስራኤል ፊት አስወጣቸው፣ ታዲያ አንተ አሁን ምድራቸውን ልትወስድ ይገባልን? 24 አምላክህ ካሞሽ የሚሰጥህን ምድር አትወስድምን? ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችን የሰጠንን ምድር ሁሉ እንወስዳለን፡፡ 25 አሁን አንተ ከሞዓብ ንጉሥ ከሴፎር ልጅ ከባላቅ በእውነት ትሻላለህን? እርሱ ከእስራኤል ጋር ከቶ ክርክር ነበረውን? ከእነርሱ ጋር ጦርነት አካሂዷልን? 26 እስራኤል በሐሴቦንና በቀበሌዎችዋ፣ በአሮዔርና በቀበሌዎችዋ፣ በአርኖንም ዳርቻ ባሉት ከተሞች ሁሉ ለሦስት መቶ ዓመት ሲኖር በነበረበት ጊዜ፣ ለምን ታዲያ በዚያን ጊዜ መልሳችሁ አልወሰዳችኋቸውም ነበር? 27 እኔ አልበደልሁህም ነገር ግን አንተ እኔን በመውጋት እየበደልከኝ ነው፡፡ ፈራጅ የሆነው እግዚአብሔር በእስራኤል ሰዎችና በአሞን ሰዎች መካከል ዛሬ ይፈርዳል፡፡ 28 ነገር ግን የአሞን ሰዎች ንጉሥ ዮፍታሔ የላከበትን ማስጠንቀቂያ አልተቀበለም፡፡ 29 ያን ጊዜ የእግዚአብሔር መንፈስ በዮፍታሔ ላይ መጣ፣ እርሱም በገለዓድና በምናሴ አለፈ፣ በገለዓድ ባለው ምጽጳም አለፈ፣ ከዚያም በገለዓድ ካለው ምጽጳ ወደ አሞን ሰዎች አለፈ፡፡ 30 ዮፍታሔም ለእግዚብሔር እንዲህ ሲል ስእለት ተሳለ፡- “በአሞንን ሰዎች ላይ ድልን ብትሰጠኝ፣ 31 ከአሞን ሰዎች በሰላም በተመለስሁ ጊዜ እኔን ሊያገኘኝ ከቤቴ በር የሚወጣው ማንኛውም ለእግዚአብሔር ይሆናል፣ እርሱንም ለሚቃጠል መሥዋዕት አቀርበዋለሁ፡፡ 32 ስለዚህ ዮፍታሔ እነርሱን ለመውጋት ወደ አሞን ሰዎች አለፈ፣ እግዚአብሔርም በእነርሱ ላይ ድል ሰጠው፡፡ 33 እርሱም ከአሮዔርም እስከ ሚኒት፣ እንደዚሁም እስከ አቤልክራሚም ድረስ ያሉ ሀያ ከተሞችን ወጋቸው፣ ታላቅ እልቂትም አደረሰባቸው፡፡ ስለዚህ የአሞን ሰዎች በእስራኤል ሰዎች ቁጥጥር ስር ሆኑ፡፡ 34 ዮፍታሄ ምጽጳ ወዳለው ቤቱ መጣ፣ በዚያም የእርሱ ልጅ ከበሮ ይዛ እያሸበሸበች ልታገኘው ወጣች፡፡ እርስዋም ብቸኛ ልጁ ነበረች፣ ከእርስዋ ሌላ ወንድ ልጅም ይሁን ሴት ልጅ አልነበረውም፡፡ 35 እርስዋንም ባየ ጊዜ፣ ልብሱን ቀደደ እንዲህም አለ፡- “ወይኔ! ልጄ ሆይ! በኀዘን አደቀቅሽኝ፣ በእኔ ላይ ጭንቅ ያመጣብኝ ሰው ሆንሽብኝ! ለእግዚአብሔር ስእለት ተስያለሁና፣ ቃሌን ማጠፍ በፍጹም አልችልም፡፡” 36 እርስዋም እንዲህ አለችው፡- “አባቴ ሆይ፣ ለእግዚአብሔር ስእለት ተስለሃል፣ ቃል የገባኸውን ሁሉ በእኔ ላይ አድርግብኝ፣ ምክንያቱም እግዚአብሔር በጠላቶችህ በአሞናውያን ላይ ተበቅሎልሃልና፡፡” 37 አርስዋም ለአባትዋ እንዲህ አለች፡- “ይህ ቃል ለእኔ ይደረግልኝ፡፡ ይህንን አካባቢ እንድለቅና ወደ ታች ወደ ኮረብታዎቹ እንድወርድ፣ ከጓደኞቼም ጋር ስለ ድንግልናየ እንዳለቅስ ለሁለት ወራቶች ያህል ብቻየን እንድሆን ፍቀድልኝ፡፡ 38 እርሱም፣ “ሂጂ” አለ፡፡ ለሁለት ወራትም አሰናበታት፡፡ እርስዋም ትታው ሄደች፣ ከባልንጀሮችዋም ጋር ስለ ድንግልናዋ በኮረብታዎቹ ላይ አለቀሱ፡፡ 39 በሁለት ወር መጨረሻ ላይ ወደ አባትዋ ተመለሰች፣ እርሱም ቃል እንደገባው እንደ ስእለቱ አደረገባት፡፡ እርስዋም ከወንድ ጋር ተኝታ አታውቅም፣ ይህም በእስራኤል ዘንድ ልማድ ሆነ፣ 40 የእስራኤል ሴቶች ልጆች በየዓመቱ፣ ለአራት ቀናት፣ የገለዓዳዊውን የዮፍታሔን ሴት ልጅ ታሪክ እየተናገሩ ያስቡአታል፡፡



Judges 11:1

ገለዓዳዊው

ይህ ከገለዓድ አውራጃ የሆነ ግለሰብ ነው። የእርሱም አባት ስም ገለዓድ መሆኑ የአጋጣሚ ጉዳይ ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የሚስቱ ወንዶች ልጆች ባደጉ ጊዜ

“የገለዓድ ሚስት የወለደቻቸው ወንዶች ልጆች በጎለመሱ ጊዜ”

በጦብ ምድር

ጦብ የአውራጃ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

መጡና ከእርሱ ጋር ሄዱ

“ተከተሉት” ወይም “አብረው በየስፍራው ሄዱ”

Judges 11:4

ከጥቂት ቀናት በኋላ

“ከጥቂት ጊዜ በኋላ”

ከእስራኤል ጋር ተዋጉ

“ተዋጉ” የሚለው ቃል የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ትርጉሙም እስራኤልን ወጉ፣ በጦርነቱም ከእነርሱ ጋር ነበሩ። እዚህ ጋ “እስራኤል” የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። (የአነጋገር ዘይቤ እና ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከ … ጋር እንድንዋጋ

“ከ -- ጋር መዋጋት እንድንችል”

Judges 11:7

ከአባቴ ቤት

እዚህ ጋ “ቤት” የሚያመለክተው በቤቱ ውስጥ ያሉትን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “ቤተሰቦቼ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አሁን ወደ አንተ የመጣነው ለዚህ ነው

“ለዚህ ነው” የሚለው ሐረግ የሚያመለክተው ዮፍታሔ በችግር ውስጥ ስለመሆናቸው የተናገረውን ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉሙ ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “አሁን ወደ አንተ የመጣነው በችግር ውስጥ ስለሆንን ነው”።

ከአሞን ሰዎች ጋር ተዋጋ

“የአሞንን ሰዎች ውጋቸው”

Judges 11:9

መሪና አዛዥ

እነዚህ ሁለት ቃላት መሰረታዊ ትርጉማቸው አንድ ሆኖ ሳለ የዮፍታሔን አስፈላጊነት አጽንዖት ለመስጠት ተደግመዋል። ሁለቱን ቃላት ልታጣምራቸው ትችላለህ። አ.ት፡ “አዛዥ”።

ዮፍታሔ በምጽጳ በእግዚአብሔር ፊት በነበረ ጊዜ የተናገረውን ቃል በሙሉ ደገመው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። እዚህ ጋ “በእግዚአብሔር ፊት” የሚለው ሐረግ የተናገረውን ቃል በአግዚአብሔር ፊት እንደ መሓላ ደገመው ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የተናገረውን ቃል በሙሉ

ይህ የሚያመለክተው መሪያቸው ለመሆን ለገለዓድ መሪዎች የተናገረውን ቃል ነው።

Judges 11:12

በመሐከላችን ያለው ይህ ጸብ ምንድነው

“በመካከላችን ለምን ጸብ ይሆናል?” ዮፍታሔ ንጉሡ በእስራኤል ላይ ለምን እንደ ተቆጣ ይጠይቃል።

መሬታችንን ለመውሰድ በኃይል የመጣኸው ለምንድነው

“አንተ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው የአሞንን ንጉሥ ሲሆን ራሱንና ወታደሮቹን ይወክላል። አ.ት፡ “ወታደሮችህ መሬታችንን ለመያዝ ለምን ይመጣሉ”

በኃይል ለመውሰድ የመጡት

“በጉልበት ለመውሰድ የመጡት”

አርኖን == ያቦቅ

እነዚህ የሁለት ወንዞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እስከ ዮርዳኖስ

“ከዮርዳኖስ ወንዝ በወዲያ በኩል”

በሰላም

“በሰላማዊ መንገድ” ወይም “ልትከላከላቸው እንዳትሞክር”

Judges 11:14

እርሱም አለ

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ለንጉሡ የሚናገረውን መልዕክተኛ ነው። ይህ ምናልባት በቡድን የሆኑትን መልዕክተኞች በሚያመለክተውና በተከፈተው ተለዋዋጭ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንዳለው “እነርሱ” ተብሎ መጻፍ ይኖርበት ይሆናል። አ.ት፡ “መልዕክተኞቹ እንዲህ እንዲሉ ዮፍታሔ ነገራቸው” ወይም “እንዲህ አሉ”።

ከግብጽ ወጥተው በመጡ ጊዜ

ሰዎች ወደ ተስፋይቱ ምድር በሚጓዙበት ጊዜ ሁሉ ወደ ተስፋይቱ ምድር “ወደ ላይ” እንደ ሄዱ ይነገርላቸዋል። እስራኤላውያን ግብፅን ለቀው በወጡ ጊዜ ወደ ተስፋይቱ ምድር በመጓዝ ላይ ነበሩ። አ.ት፡ “ግብፅን ለቀው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 11:17

እስራኤል መልዕክተኞችን በላኩ ጊዜ

መልዕክተኞቹ የተላኩት በእስራኤል መሪዎች ናበር። አ.ት፡ “የእስራኤል መሪዎች መልዕክተኞችን በላኩ ጊዜ”

በሚያልፉበት

“በመሐል ሲሄዱ” ወይም “ማቋረጥ”

አልሰማም

ይህ ቃል ዘይቤአዊ አነጋገር ሲሆን ትርጉሙም “እምቢ” ማለት ነው። አ.ት፡ “እምቢ አለ” ወይም “ጥያቄአቸውን አልተቀበለም” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ደግሞም ወደ ሞዓብ ንጉሥ መልዕክተኞችን ላኩ

እስራኤል ወደ ሞዓብ ንጉሥ መልዕክተኞችን የላኩበት ምክንያት ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ደግሞም ወደ ሞዓብ ንጉሥ ተመሳሳዩን ጥያቄ የሚያቀርቡ መልዕክተኞችን ላኩ”

እርሱ ግን እምቢ አለ

እስራኤል በሞዓብ መካከል ለማለፍ ያቀረበውን ጥያቄ የሞዓብ ንጉሥ አልተቀበለውም። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በበለጠ ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እርሱም ደግሞ እምቢ አለ፣ በሞዓብ ምድር መካከል እንዲያልፉም አልፈቀደላቸውም”።

አርኖን

ይህ የወንዝ ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 11፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Judges 11:19

እስራኤል ወደ ሴዎን መልዕክተኞችን ላኩ

መልዕክተኞቹ የተላኩት በእስራኤል መሪዎች ነው። አ.ት፡ “የእስራኤል መሪዎች መልዕክተኞችን በላኩ ጊዜ”

ሴዎን

ይህ የሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሐሴቦን -- ያሃድ

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሴዎን ግን እስራኤል በግዛቱ ውስጥ ያልፍ ዘንድ አላመነውም

ሴዎን በምድሩ በሰላም ያልፋል ብሎ እስራኤልን አላመነም። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በይበልጥ ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ይሁን እንጂ ሴዎን የእስራኤል ሕዝብ በግዛቱ በኩል በሰላም ያልፋል ብሎ አላመነም”።

በዚያ ተዋጋቸው

“እርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ሴዎንን ሲሆን ይህም ራሱንና ሰራዊቱን ይወክላል። አ.ት፡ “በዚያ ተዋጉ” ወይም “በዚያ ሰራዊቱ ተዋጋ”

Judges 11:21

ሴዎን

የዚህን ሰው ስም በመሳፍንት 11፡19 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሴዎንና ሕዝቡን ሁሉ በእስራኤል እጅ ሰጠ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚያመለክተው በጦርነት የማሸነፍ ኃይልን ነው። አ.ት፡ “በሴዎንና በሕዝቡ ሁሉ ላይ ለእስራኤል ኃይልን ሰጠው”። (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አርኖን -- ያቦቅ

የእነዚህን ወንዞች ስም በመሳፍንት 11፡13 ላይ እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

Judges 11:23

አሁን መሬታቸውን የራስህ አድርገህ ትወስዳለህ?

ዮፍታሔ ምላሽ በማይፈልግ በዚህ ጥያቄ የአሞናውያንን ንጉሥ ይገስጸዋል። “የእነርሱ” የሚለው ቃል እስራኤልን ያመለክታል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በመሆኑም፣ መሬታቸውን የራስህ አድርገህ መውሰድ አይኖርብህም”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አምላክህ ካሞሽ የሚሰጥህን ምድር አትወስድም?

ዮፍታሔ ምላሽ በማይሻ ጥያቄ የአሞናውያንን ንጉሥ እየገሰጸው ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “አምላክህ ካሞሽ የሚሰጥህን ምድር ብቻ መውሰድ ይኖርብሃል”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ውሰድ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ትርጉሙ አንድን ነገር በቁጥጥር ስር ማድረግ ማለት ነው። አ.ት፡ “በቁጥጥርህ ስር አድርግ” ወይም “የራስህ አድርግ”። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ካሞሽ

ይህ የሐሰተኛ አምላክ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አሁን አንተ ከሞዓብ ንጉሥ ከሴፎር ልጅ ከባላቅ በእርግጥ ትበልጣለህ?

ዮፍታሔ ምላሽ በማይሻ ጥያቄ የአሞናውያንን ንጉሥ እየገሰጸው ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “አንተ የሞዓብ ንጉሥ ከነበረው ከሴፎር ልጅ ከባላቅ አትሻልም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ባላቅ -- ሴፎር

እነዚህ የሰዎች ስምች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከእስራኤል ጋር ለመከራከር ደፍሯል?

ዮፍታሔ ምላሽ በማይሻ ጥያቄ የአሞናውያንን ንጉሥ እየገሰጸው ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ይሁን እንጂ ከእስራኤል ጋር ለመከራከር አልደፈረም”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

በእነርሱስ ላይ ጦርነትን ዐውጇል?

ዮፍታሔ ምላሽ በማይሻ ጥያቄ የአሞናውያንን ንጉሥ እየገሰጸው ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ከቶ በእነርሱ ላይ ጦርነትን አላወጀም”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

Judges 11:26

ሦስት መቶ ዓመት

“300 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሐሴቦን

በመሳፍንት 11፡19 ላይ በተረጎምክበት መልኩ የዚህችን ከተማ ስም ተርጉም።

አሮዔር

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

አርኖን

በመሳፍንት 11፡13 ላይ በተረጎምክበት መልኩ የዚህችን ከተማ ስም ተርጉም።

ታዲያ በዚያን ጊዜ ለምን አላስመለስካቸውም?

ዮፍታሔ ምላሽ በማይሻ ጥያቄ የአሞናውያንን ንጉሥ እየገሰጸው ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “በዚያን ጊዜ ማስመለስ ነበረብህ” ወይም “ከአመታት በፊት ልታስመልሳቸው ይገባህ ነበር፤ አሁን ግን በጣም ዘግይተሃል” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

እኔ አልበደልኩህም፣ አንተ ግን እየወጋኸኝ በድለኸኛል

ዮፍታሔ የሚናገረው ሴዎንን ነው። እዚህ ጋ፣ ዮፍታሔ፣ ራሱን እንደ እስራኤላውያን፣ ንጉሣቸውን ሴዎንን እንደ አሞናውያን አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “እስራኤላውያን ሕዝብህን አልበደሉም፣ ይሁን እንጂ ሕዝብህ እየወጉን በድለውናል”።

አልበደልኩህም -- በድለኸኛል

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አንድን ሰው መበደል ማለት እነርሱን መበደል ነው። አ.ት፡ “የማይገባውን አላደረግሁብህም … የማይገባውን አድርገህብኛል” ወይም “ኢፍትሐዊ አልሆንኩብህም … ኢፍትሐዊ ሆነህብኛል”። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 11:29

የእግዚአብሔር መንፈስ በዮፍታሔ ላይ መጣበት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ትርጉሙም በዮፍታሔ ውሳኔዎች ላይ መንፈስ ቅዱስ ተጽዕኖ አሳድሯል ማለት ነው። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር መንፈስ ዮፍታሔን ተቆጣጠረው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከገለዓድ ምጽጳ -- በገለዓድና በምናሴ መሐል አለፈ

ዮፍታሔ በእነዚህ አካባቢዎች ከአሞን ሰዎች ጋር ለሚያደርገው ውጊያ ሰዎችን በሰራዊቱ ውስጥ ለማካተት እየመዘገባቸው አለፈ። የዚህ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከምጽጳ ገለዓድ … ሰዎችን ወደ ሰራዊቱ እየሰበሰበ በገለዓድና ምናሴ መካከል አለፈ”።

እሠዋዋለሁ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ትርጉሙ አንድን ነገር መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ ማለት ነው። አ.ት፡ “እርሱን እሠዋልሃለሁ” ወይም “መሥዋዕት አድርጌ አቀርብልሃለሁ”። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 11:32

ስለዚህ ዮፍታሔ አለፈ -- ተዋጋ - እግዚአብሔር ድልን ሰጠው

ዮፍታሔ የሰራዊቱ መሪ በመሆኑ፣ እርሱና ሰራዊቱ በተደጋጋሚ ዮፍታሔን ራሱን ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ስለዚህ ዮፍታሔና ሰራዊቱ አለፉ -- ተዋጉ -- እግዚአብሔር ድልን ሰጣቸው”

አሮኤር

የዚህችን ከተማ ስም በመሳፍንት 11፡26 ላይ በተረጎምክበት መልኩ ተርጉም።

ሚኒት -- አቤል ክራሚም

እነዚህ የከተሞች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሃያ ከተሞች

“20 ከተሞችን ጨምሮ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 11:34

አታሞ

እንደ ከበሮ የሚመታበት አናት ያለው፣ በሚንቀሳቀስበት ጊዜ ድምፅ እንዲያሰማ በዙሪያው ቁርጥራጭ ብረቶች የሚደረጉለት የሙዚቃ መሣሪያ።

ልብሶቹን ቀደደ

ይህ ለቅሶን ወይም ታላቅ ሐዘንን የሚያሳይ ድርጊት ነው። አ.ት፡ “ልብሱን በሐዘን ቀደደ” (ምሳሌአዊ ድርጊት የሚለውን ተመልከት)

በሐዘን ሰበርሽኝ -- ለህመም ዳረግሽኝ

ዮፍታሔ አንዱን አሳብ ሁለት ጊዜ መናገሩ እጅግ ስለ ማዘኑ አጽንዖት ለመስጠት ነው።

በሐዘን ሰበርሽኝ

እዚህ ጋ፣ ዮፍታሔ ጥልቅ ሐዘኑን እንደሚሰባብረው አንደ አንዳች ነገር ቆጥሮ ይናገራል። አ.ት፡ “ጥልቅ ሐዘን ላይ ጥለሽኛል” ወይም “በሐዘን እንድሞላ አደረግሽኝ”። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለህመም ዳረግሽኝ

እዚህ ጋ ዮፍታሔ የሚናገረው ጥልቅ ሐዘኑና ሥቃዩ እንደ ሕመም እንደሆነበት ነው። አ.ት፡ “አንቺ ሥቃይ እንደሚያመጣብኝ ዓይነት ሰው ሆነሻል” ወይም “ለጥልቅ ሐዘን ዳርገሽኛል”። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ቃሌን ማጠፍ አልችልም

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ቃልን ማጠፍ ማለት ልታደርገው ቃል የገባህበትን ጉዳይ መተው ነው። አ.ት፡ “ቃል የገባሁበትን ጉዳይ መፈጸም አለብኝ” ወይም “ቃሌን ለማጠፍ አልችልም”። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 11:36

ጠላቶችህን አሞናውያንን ተበቅሎልሃልና

ጠላቶቹን በማሸነፍ እግዚአብሔር ተበቅሎለታል። የዚህ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በጠላቶችህ በአሞናውያን ላይ ተበቅሎልሃል”

ይህ ቃል ኪዳን ይጠበቅልኝ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስለ እኔ ይህንን ቃል ኪዳን ጠብቅ” ወይም “እኔን በሚመለከት ይህንን ቃል ኪዳን ጠብቅ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ስለ ድንግልናዬ ላልቅስ

“ድንግል በመሆኔ ምክንያት ላልቅስ” ወይም “ከእንግዲህ ስለማላገባ ላልቅስ”

Judges 11:38

ገለዓዳዊው

ይህ አንድን ከገለዓድ የሆነን ሰው ያመለክታል። ይህንን በመሳፍንት 10፡3 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።


Chapter 12

1 ወደ ኤፍሬም ሰዎችም ጥሪ ደረሰ፤ በጻፎን በኩል ተሻግረው ዮፍታሔን፣ “ከአሞን ሕዝብ ጋር ለመዋጋት ስታልፍ ከአንተ ጋር እንድንሄድ ያልጠራኸን ለምድን ነው? ቤትህን በአንተ ላይ እናቃጥለዋለን” አሉት፡፡ 2 ዮፍታሔም እንዲህ አላቸው፣ “እኔና ሕዝቤ ከአሞን ሕዝብ ጋር በታላቅ ጦርነት ውስጥ ነበርን፡፡ በጠራኋችሁም ጊዜ ከእነርሱ አላዳናችሁኝም፡፡ 3 እናንተም እንዳላዳናችሁኝ ባየሁ ጊዜ፣ ሕይወቴን በራሴ ብርታት አስቀምጬ በአሞን ሕዝብ ላይ ለመዋጋት አለፍሁ፣ እግዚአብሔርም በእነርሱ ላይ ድል ሰጠኝ፡፡ ዛሬ እኔን ለመውጋት ለምን መጣችሁ? 4 ዮፍታሔም የገለዓድን ሰዎች ሁሉ ሰበሰበና ከኤፍሬምም ጋር ተዋጋ፡፡ የገለዓድም ሰዎች የኤፍሬምን ሰዎች ወጓቸው ምክንቱም፣ “እናንተ ገለዓዳውያን በኤፍሬም ውስጥ ሸሽታችሁ የተጠጋችሁ፣ በኤፍሬምና በምናሴ ውስጥ ጥገኞች የሆናችሁ ናችሁ” ይሏቸው ነበርና፡፡ 5 ገለዓዳውያንም ወደ ኤፍሬም የሚወስደውን የዮርዳኖስን መሻገሪያ ያዙባቸው፡፡ አምልጦ የሚሸሽ የኤፍሬም ሰው፣ “ወንዙን ተሻግሬ ልለፍ” ባለ ጊዜ፣ የገለዓድ ሰዎች ደግሞ እንዲህ ይሉታል፣ “አንተ ኤፍሬማዊ ነህን?” እርሱም፣ “አይደለሁም” ቢል፣ 6 እነርሱም “ሺቦሌት በል” ይሉታል፡፡ እርሱም “ሲቦሌት” ብሎ ከተናገረ (ምክንያቱም እርሱ ቃሉን አጥርቶ መናገር አይችልምና) ፣ ገለዓዳውያን እርሱን ይዘው በዮርዳኖስ መሻገሪያ ላይ ይገድሉታል፡፡ በዚያም ጊዜ አርባ ሁለት ሺህ ኤፍሬማውያን ተገደሉ፡፡ 7 ዮፍታሔም በእስራኤል ላይ ለስድስት ዓመት እንደ ፈራጅ አገለገለ፡፡ ከዚያም ገለዓዳዊውም ዮፍታሔ ሞተ፣ ከገለዓድ ከተሞችም በአንዱ ተቀበረ። 8 ከእርሱም በኋላ የቤተ ልሔሙ ኢብጻን በእስራኤል ላይ እንደ ፈራጅ አገለገለ፡፡ 9 እርሱም ሠላሳ ወንዶች ልጆች ነበሩት፡፡ ሠላሳ ሴቶች ልጆችንም ወደ ውጭ በትዳር ለሌሎች ሰጠ፣ ሠላሳ ሴቶች ልጆችን ደግሞ ከሌሎች ሰዎች በትዳር ለወንድ ልጆቹ አመጣ። በእስራኤልም ላይ ለሰባት ዓመት ፈረደ። 10 ኢብጻንም ሞተ፣ በቤተ ልሔምም ተቀበረ፡፡ 11 ከእርሱም በኋላ ዛብሎናዊው ኤሎም በእስራኤል ላይ እንደ ፈራጅ አገለገለ፡፡ እርሱም በእስራኤል ላይ ለአሥር ዓመት ፈረደ፡፡ 12 ዛብሎናዊውም ኤሎም ሞተ፣ በዛብሎንም ምድር ባለችው በኤሎም ተቀበረ፡፡ 13 ከእርሱም በኋላ የጲርዓቶናዊው የሂሌል ልጅ ዓብዶን በእስራኤል ላይ እንደ ፈራጅ አገለገለ፡፡ 14 እርሱም አርባ ወንዶች ልጆችና ሠላሳ ወንዶች የልጅ ልጆች ነበሩት፡፡ በሰባ አህያዎች ላይ ይጋልቡ ነበር፣ እርሱም በእስራኤል ላይ ለስምንት ዓመት ፈረደ፡፡ 15 የጲርዓቶናዊውም የሂሌል ልጅ ዓብዶን ሞተ፣ በተራራማውም በአማሌቃውያን አገር በኮረብታማው በኤፍሬም አገር ውስጥ ባለችው በጲርዓቶን ውስጥ ተቀበረ፡፡



Judges 12:1

ለኤፍሬም ሰዎች ጥሪ ደረሳቸው

እዚህ ጋ “ጥሪ” የሚለው የነገር ስም እንደ ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የኤፍሬም ሰዎች በአንድ ላይ ተጠሩ” ወይም “የኤፍሬም ሰዎች ወታደሮቻቸውን በአንድ ላይ ሰበሰቧቸው”። (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ጻፎን

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ተሻገሩ -- አለፉ

“መንገዳቸውን … አልፈው ሄዱ” ወይም “ጉዞአቸውን … አልፈው ተጓዙ”

ቤትህን በላይህ ላይ እናቃጥለዋለን

ይህ የአነጋገር ዘይቤ የሚያመለክተው ቤቱን በውስጡ ካሉት ሰዎች ጋር ስለ ማቃጠል ነው። አ.ት፡ “ቤትህን በውስጡ እንዳለህ እናቃጥለዋለን”። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እናንተን በጠራዃችሁ ጊዜ

እዚህ ጋ “እናንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ሲሆን የሚያመለክተው የኤፍሬምን ሰዎች ነው።

አላዳናችሁኝም

ዮፍታሔ “እኔ” የሚለውን ቃል የሚጠቀመው ራሱንና የገለዓድን ሰዎች በሙሉ ለማመልከት ነው። አ.ት፡ “አታድኑን”

Judges 12:3

እናንተ አላዳናችሁኝም

“እናንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ሲሆን የኤፍሬምን ሰዎች ያመለክታል። ዮፍታሔ “እኔ” በሚልበት ጊዜ የሚያመለክተው ራሱን ጨምሮ የገለዓድን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “አላዳናችሁንም”።

ሕይወቴን በእጄ ጥዬ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ በራስ ጉልበት በመደገፍ ራስን ለአደጋ መስጠት ማለት ነው። ዮፍታሔ የገለዓድን ሰዎች እንደ ራሱ አድርጎ ማመልከቱን ይቀጥላል። አ.ት፡ “በራሳችን በመተማመን ሕይወታችንን ለአደጋ ሰጥተናል”። (የአነጋገር ዘይቤ እና የሚለውን ተመልከት)

እግዚአብሔር ድልን ሰጥቶኛል

በአሞናውያን ላይ እግዚአብሔር ለገለዓድ ሰዎች ድልን እንደ ሰጣቸው ዮፍታሔ ያመላክታል። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም በይበልጥ መብራራት ይችላል። አ.ት፡ “በእነርሱ ላይ እግዚአብሔር ድልን ሰጥቶናል” ወይም “በጦርነት እንድናሸንፋቸው እግዚአብሔር ፈቅዶልናል”

ከኤፍሬም ጋር ተዋጋ

“እርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ዮፍታሔንና የገለዓድን ተዋጊዎች ሁሉ ነው። አ.ት፡ “ከኤፍሬም ጋር ተዋጉ”

ለምን ልትወጉኝ መጣችሁ

“እናንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ሲሆን የሚያመለክተው የኤፍሬምን ሰዎች ነው። ዮፍታሔ “እኔ” በሚልበት ጊዜ የሚያመለክተው ራሱን ጨምሮ የገለዓድን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “እኛን ልትወጉን ለምን መጣችሁ”

ገለዓዳውያን ኮብላዮች ናቸው

የዚህን ስድብ ትርጉም ግልጽ ልታደርገው ትችላለህ። አ.ት፡ “ይህ ቦታ ለእናንተ ለገለዓዳውያን አይገባችሁም። እናንተ በዚህ ለመኖር የመጣችሁ ሰዎች ብቻ ናችሁ”

በአሞን ሰዎች ላይ አልፈው ሄዱ

ይህ ማለት በአሞን በኩል ሲያልፉ ከአሞናውያን ጋር ተዋጉ። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በግዛታቸው በኩል ስናልፍ ክአሞን ሰዎች ጋር ተዋጋን”

ገለዓዳውያን

የገለዓድ ሰዎች

በኤፍሬም -- በኤፍሬምና በምናሴ

“በኤፍሬምና በምናሴ አውራጃዎች” ወይም “በኤፍሬምና በምናሴ ምድር”። እዚህ ጋ “ኤፍሬም” እና “ምናሴ” የሚያመለክቱት አውራጃዎችን ሲሆን በዚያ በሚኖሩ ነገዶች ስም ተሰይመዋል።

Judges 12:5

ለኤፍሬም

“ለኤፍሬም ምድር”

ገለዓዳውያን ያዙት

“ገለዓዳውያን ተቆጣጠሩት” ወይም “ገለዓዳውያን ያዙት”

መልካ

እነዚህ ውሃው ጥልቀት የሌለው በመሆኑ በእግር ልታቋርጥ የምትችለው ወንዝ ያሉባቸው አካባቢዎች ናቸው።

ኤፍሬማዊ

ከኤፍሬም ነገድ የሆነ ሰው

ሺቦሌት -- ሲቦሌት

እነዚህ ቃላት ምንም ትርጉም የላቸውም። እነዚህን ቃላት ወደ ራስህ ቋንቋ ቅዳቸውና በቃላቱ መጀመሪያ ላይ “ሺ” እና “ሲ” የሚሉ ፊደላት ለየብቻ መተርጎማቸውን እርግጠኛ ሁን። (ቃላትን መቅዳት ወይም መዋስ የሚለውን ተመልከት)

ቃሉን መናገር

“የቃላቱን ድምፅ ማውጣት”

አርባ ሁለት ሺህ

“42,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አርባ ሁለት ሺህ ኤፍሬማውያን ተገደሉ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አርባ ሁለት ሺህ ኤፍሬማውያንን ገደሉ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 12:7

ገለዓዳዊው ዮፍታሔ ሞተና ተቀበረ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ገለዓዳዊው ዮፍታሔ ሞተና ቀበሩት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 12:8

የቤተ ልሔሙ ኢብጻን

ይህ ከቤተ ልሔም የሆነ የአንድ ሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ ሠላሳ ሴቶች ልጆቹን ዳረ

እዚህ ጋ “ዳረ” የሚለው ቃል የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ልጆቹ እንዲያገቡ ፈቅዷል ማለት ነው። አ.ት፡ “ሠላሳ ሴቶች ልጆች ነበሩትና እያንዳንዳቸው እንዲያገቡ ቅድመ ዝግጅት አደረገላቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ለወንዶች ልጆቹም ከውጭ ከሌሎች ሰዎች ሠላሳ ሴቶች ልጆችን አመጣላቸው

“ከውጭ አመጣላቸው” የሚለው የአነጋገር ዘይቤ ትርጉሙ ከሌላ ጎሳ የሆኑት ሴቶች ከወንዶች ልጆቹ ጋር ተጋቡ ማለት ነው። አ.ት፡ “ከራሱ ጎሳ ውጭ ካሉ ሰዎች ሠላሳ ሴቶች ልጆች የእርሱን ወንዶች ልጆች እንዲያገቡ አደረገ”። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 12:10

በቤተ ልሔም ተቀበረ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በቤተ ልሔም ቀበሩት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ኤሎን

ይህ የሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዛብሎናዊ

ከዛብሎን ነገድ የሆነ አንድ ሰው

ኢያሎን

የዚህን ቦታ ስም በመሳፍንት 1፡35 ላይ እንደተረጎምከው ተርጉመው።

በኢያሎን ተቀበረ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በኢያሎን ቀበሩት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 12:13

አብዶን --ሂሌል

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ጲርዓቶናዊው -- ጲርዓቶን

ጲርዓቶን የቦታ ስም ሲሆን ከዚያ አካባቢ የሆነ ሰው ደግሞ ጲርዓቶናዊ ይባላል። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በሰባ አህዮች የሚቀመጡ

እነዚህ ሰዎች የሚቀመጡባቸውን ሰባ አህዮች የራሳቸው ማድረግ ችለዋል። እዚህ ጋ “መቀመጥ” የሚለው ቃል “የራስ ማድረግ” ከሚለው ይልቅ ጥቅም ላይ ውሏል። አ.ት፡ “ሰባ አህዮች ነበሯቸው” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አርባ ወንዶች ልጆች -- ሠላሳ የልጅ ልጆች -- ሰባ አህዮች

“40 ወንዶች ልጆች -- 30 የልጅ ልጆች -- 70 አህዮች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)


Chapter 13

1 የእስራኤልም ሕዝብ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን ስራ እንደ ገና ሠሩ፣ እርሱም ፍልስጥኤማውያን በእነርሱ ላይ ለአርባ ዓመት እንዲገዙ ፈቀደላቸው፡፡ 2 ከዳን ቤተሰብ የሆነ ስሙም ማኑሄ የሚባል አንድ የጾርዓ ሰው ነበረ፡፡ ሚስቱም መካን ስለነበረች ልጅ አልወለደችም፡፡ 3 የእግዚአብሔርም መልአክ ለሴቲቱ ተገልጦ እንዲህ አላት፣ “ተመልከቺ፣ አንቺ መካን ነበርሽ፣ ልጅም አልወለድሽም፣ ነገር ግን ትፀንሻለሽ፣ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፡፡ 4 አሁንም የወይን ጠጅ ወይም የሚያሰክር ጠንካራ መጠጥ እንዳትጠጪ ተጠንቀቂ፣ ሕጉ ርኩስ እንደሆነ የገለጸውን ማንኛውንም ምግብ አትብዪ፡፡ 5 ተመልከቺ፣ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፡፡ ልጁ ከአንቺ ማኅፀን ጀምሮ ለእግዚአብሔር የተለየ ናዝራዊ ስለሚሆን በራሱ ላይ ምላጭ አይድረስበት፡፡ እርሱም እስራኤልን ከፍልስጥኤማውያን ጉልበት ማዳን ይጀምራል፡፡ 6 የዚያን ጊዜ ሴቲቱ ወደ ባልዋ መጥታ እንዲህ ብላ ነገረችው፣ “አንድ የእግዚአብሔር ሰው ወደ እኔ መጣ፣ መልኩም እንደ እግዚአብሔር መልአክ የሚመስል ነበረ፣ በጣምም አስደነገጠኝ፡፡ ከወዴት እንደ መጣ አልጠየቅሁትም፣ እርሱም ስሙን አልነገረኝም፡፡ 7 እርሱም እንዲህ አለኝ፣ ‘ተመልከቺ! ትፀንሻለሽ፣ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፡፡ ስለዚህ ልጁ ከአንቺ ማኅፀን ጀምሮ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ ለእግዚአብሔር የተለየ ናዝራዊ ስለሚሆን የወይን ጠጅ ወይም የሚያሰክር ጠንካራ መጠጥ እንዳትጠጪ፣ ሕጉ ርኩስ እንደሆነ የገለጸውን ማንኛውንም ምግብ አትብዪ፡፡’” 8 ከዚያም ማኑሄ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ሲል ጸለየ፣ “ጌታ ሆይ፣ አሁን በቅርቡ ለሚወለደው ልጅ ምን ማድረግ እንዳለብን እንዲያስተምረን እባክህ የላክኸው የእግዚአብሔር ሰው እንደገና ወደ እኛ ይምጣ፡፡” 9 እግዚአብሔርም የማኑሄን ጸሎት መለሰ፣ የእግዚአብሔርም መልአክ እንደ ገና ወደ ሴቲቱ በእርሻ ውስጥ ተቀምጣ ሳለች መጣ፡፡ ነገር ግን ባልዋ ማኑሄ ከእርስዋ ጋር አልነበረም፡፡ 10 ስለዚህ ሴቲቱም ፈጥና ሮጠችና ለባልዋ ነገረችው፣ “ተመልከት! በሌላኛው ቀን ወደ እኔ የመጣው ሰው እንደገና ተገለጠልኝ፡፡” 11 ማኑሄም ተነሳና ሚስቱን ተከተላት፡፡ ወደ ሰውዮውም በመጣ ጊዜ እንዲህ አለው፣ “ከሚስቴ ጋር የተነጋገርህ ሰው አንተ ነህን?” ሰውየውም፣ “እኔ ነኝ” አለው፡፡ 12 ስለዚህ ማኑሄ እንዲህ አለ፣ “አሁንም ቃሎችህ እውነት ይሁኑ፡፡ ነገር ግን ልጁ የሚመራው በምንድን ነው፣ እኛስ ለእርሱ የምንሰራው ምንድን ነው?” 13 የእግዚአብሔርም መልአክ ለማኑሄ እንዲህ አለው፣ “እርስዋ የነገርኋትን ነገር ሁሉ በጥንቃቄ ማድረግ አለባት፡፡ 14 ከወይን ከሚወጣው ማንኛውንም ነገር አትብላ፣ የወይን ጠጅ ወይም የሚያሰክር ሌላ ጠንካራ መጠጥ አትጠጣ፤ ሕጉ ርኩስ ነው ብሎ የገለጸውን ማንኛውንም ምግብ አትብላ፡፡ እኔ እንድታደርገው ያዘዝኋትን ማንኛውንም ነገር መታዘዝ አለባት፡፡ 15 ማኑሄም ለእግዚአብሔር መልአክ እንዲህ አለው፣ “ለአንተ የፍየል ጠቦት ለማዘጋጀት ጊዜ እናገኝ ዘንድ፣ እባክህ ለአጭር ጊዜ ቆይ፡፡” 16 የእግዚአብሔርም መልአክ ለማኑሄ እንዲህ አለው፣ “ብቆይም እንኳ፣ መብልህን አልበላም፡፡ነገር ግን የሚቃጠል መሥዋዕት የምታዘጋጅ ከሆነ፣ ያንን ለእግዚአብሔር አቅርበው፡፡” ማኑሄ የእግዚአብሔር መልአክ መሆኑን አላወቀም ነበር፡፡ 17 ማኑሄም ለእግዚአብሔር መልአክ እንዲህ አለው፣ “የተናገርሃቸው ቃሎች እውነት በሆኑ ጊዜ እናከብርህ ዘንድ ስምህ ማን ነው?” 18 የእግዚአብሔርም መልአክ እንዲህ አለው፣ “ስሜን ለምን ትጠይቃለህ? ስሜ ድንቅ ነው!” 19 ስለዚህ ማኑሄም የፍየሉን ጠቦት ከእህል ቍርባን ጋር ወሰደና በድንጋይ ላይ ለእግዚአብሔር አቀረበው፡፡ ማኑሄና ሚስቱ እያዩ እርሱ አስደናቂ ነገር አደረገ፡፡ 20 ነበልባሉም ከመሠዊያው ላይ ወደ ሰማይ በወጣ ጊዜ፣ የእግዚአብሔር መልአክ በመሠዊያው ነበልባል ውስጥ ወደ ላይ ዐረገ፡፡ ማኑሄና ሚስቱም ይህን ተመለከቱና በግምባራቸው ምድር ላይ ተደፉ፡፡ 21 የእግዚአብሔርም መልአክ ላማኑሄ ወይም ለሚስቱ እንደገና አልተገለጠም፡፡ ያን ጊዜም ማኑሄ የእግዚአብሔር መልአክ መሆኑን አወቀ፡፡ 22 ማኑሄም ለሚስቱ እንዲህ አላት፣ “እግዚአብሔርን ስላየን በእርግጠኝነት እንሞታለን፡፡” 23 ነገር ግን ሚስቱ እንዲህ አለችው፣ “እግዚአብሔር ሊገድለን ቢፈልግ ኖሮ፣ ለእርሱ ያቀረብነውን የሚቃጠለውን መሥዋዕትና የእህሉን ቍርባን ባልተቀበለን ነበር፡፡ ይህንም ነገር ሁሉ ባላሳየን ነበር፣ በዚህ ጊዜ እንዲህ ያሉ ነገሮችንም እንድንሰማ ባላደረገን ነበር፡፡” 24 ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ሴቲቱ ወንድ ልጅ ወለደች፣ ስሙንም ሳምሶን ብላ ጠራችው፡፡ ልጁም አደገ እግዚአብሔርም ባረከው፡፡ 25 የእግዚአብሔርም መንፈስ እርሱን በጾርዓና በኤሽታኦል መካከል ባለው በዳን ሰፈር ውስጥ ያነቃቃው ጀመር፡፡



Judges 13:1

በእግዚአብሔር ፊት ክፉ የሆነውን

የእግዚአብሔር ፊት የእርሱን ፍርድ ወይም ምዘና ይወክላል። ይህንን በመሳፍንት 2፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “በእግዚአብሔር ፍርድ ክፉ የሆነውን” ወይም “እግዚአብሔር ክፉ ነው ያለውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በፍልስጥኤማውያን እጅ ሰጣቸው

እዚህ ጋ “እጅ” የሚወክለው በጦርነት ድል ማድረጊያ ኃይልን ነው። አ.ት፡ “ፍልስጥኤማውያን እንዲያሸንፏቸው ፈቀደ” ወይም “በፍልስጥኤማውያን እንዲጨቆኑ ፈቀደ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አርባ ዓመት

“40 ዓመት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ጾርዓ

ይህ በእስራኤል የነበረ ከተማ ስም ነው። እርሱ በዳን ድንበር አቅራቢያ በይሁዳ አውራጃ ነበር። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ዳናውያን

የዳን ነገድ ሰዎች

ማኑሄ

ይህ የሰው ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 13:3

ወንድ ልጅ ትወልጃለሽ

ይህ የሕፃን ልጅን መወለድ ያመለክታል። አ.ት፡ “ወንድ ልጅ መውለድ” ወይም “ወንድ ሕፃን ልጅ ይኖርሻል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕ ያልሆነ ምንም ነገር

እግዚአብሔር መበላት የለበትም ያለው ነገር በአካላዊነቱም ንጹሕ እንዳይደለ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እነሆ

“አስተውይ” ወይም “አድምጪ”

በራሱ ላይ ምላጭ አያርፍበትም

እዚህ ጋ “ራስ” የሚያመለክተው ጸጉሩን ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ማንም ጸጉሩን እንዳይቆርጠው”(አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ምላጭ

ጸጉርን ከቆዳ አጠገብ አድርሶ ለመቁረጥ የሚያገለግል ስል ቢለዋ ነው

ለእግዚአብሔር ናዝራዊ

ይህ ማለት እንደ ናዝራዊ ለእግዚአብሔር የተሰጠ ይሆናል ማለት ነው። አ.ት፡ “ለእግዚአብሔር የተሰጠ ናዝራዊ” ወይም “እንደ ናዝራዊ ለእግዚአብሔር የተሰጠ”

ከማህፀን

እዚህ ጋ “ማህፀን” የሚያመለክተው ሕፃን ከመወለዱ በፊት ያለውን ጊዜ ነው። አ.ት፡ “ከመወለዱ በፊት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከፍልስጥኤማውያን እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” መቆጣጠር ማለት ነው። አ.ት፡ “ከፍልስጥኤማውያን ቁጥጥር” ወይም “በፍልስጥኤማውያን ቁጥጥር ስር ከመሆን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 13:6

አንድ የእግዚአብሔር ሰው

ይህ ማለት ሰውየው የተላከው በእግዚአብሔር ነው። ይህ ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር የላከው አንድ ሰው”

መልኩ በጣም የሚያስፈራ እንደ እግዚአብሔር መልአክ ነበር

እዚህ ጋ “በጣም የሚያስፈራ” ማለት “አስደንጋጭ” ማለት ነው። አ.ት፡ “የእግዚአብሔርን መልአክ ይመስል ስለ ነበረ በጣም ፈርቼ ነበር”

እነሆ

“አስተውል” ወይም “አድምጥ”

ወንድ ልጅ ትወልዳለች

ይህ የሕፃን ልጅ መወለድን ያመለክታል። አ.ት፡ “ወንድ ልጅ ትወልዳለች” ወይም “ወንድ ሕፃን ልጅ ይኖራታል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የትኛውንም በሕጉ ንጹህ ያልተባለውን ምግብ

እግዚአብሔር መበላት የለበትም ያለው ነገር በአካላዊነቱም ንጹሕ እንዳይደለ ተነግሯል። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ለእግዚአብሔር ናዝራዊ

ይህ ማለት እንደ ናዝራዊ ለእግዚአብሔር የተሰጠ ይሆናል። ይህንን በመሳፍንት 3፡5 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ለእግዚአብሔር የተሰጠ ናዝራዊ” ወይም “እንደ ናዝራዊ ለእግዚአብሔር የተሰጠ”

በማህፀንሽ ከተፀነሰበት እስከሚሞትበት ጊዜ ድረስ

ይህ አጽንዖት የሚሰጠው በሕይወት ዘመኑ ሁሉ መሆን እንዳለበት ነው። አ.ት፡ “ሕይወቱን ሙሉ”

Judges 13:8

ማኑሄ

የዚህን ሰውዬ ስም በመሳፍንት 13፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ወደ ሴቲቱ መጣ

ግልጽ ያልሆኑትን የዳራውን ቃላት ግልጽ ልታደርጋቸው ትችላለህ። አ.ት፡ “ወደ ማኑሄ ሚስት መጣ”

Judges 13:10

እነሆ

“ስማ” ወይም “የምነግርህን ልብ በል”

ሰውየው

ይህ በመሳፍንት 13፡3 የእግዚአብሔርን መልአክ ያመለክታል። ይህ ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር ሰው”

Judges 13:12

ቃሎችህ

“የተናገርከው ቃል”

የትኛውንም ከወይን የሚገኘውን

እዚህ ጋ መልአኩ ከወይን “የሚወጣ” ሲል የትኛውንም ከወይን የሚገኘውን ምግብ እንደሆነ ያመላክታል። አ.ት፡ “በወይን ላይ የሚበቅል ማንኛውም ነገር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ንጹሕ ያልሆነ

እግዚአብሔር መበላት የለበትም ያለው ነገር በአካላዊነቱም ንጹሕ እንዳይደለ ተነግሯል። ይህንን ሐረግ በመሳፍንት 13፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 13:15

የፍየል ጠቦት ይዘጋጅልህ

ግልጽ ያልሆነውን የማኑሄን መግለጫ ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “እንድትበላው የፍየል ጠቦት እናብስልልህ”

Judges 13:17

ቃሎችህ ሲፈጸሙ

“የተናገርከው ሲፈጸም”

ስሜን ለምን ትጠይቃለህ?

መልአኩ በተግሳጽ መልክ ይህንን ጥያቄ ይጠይቃል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስሜ ማን መሆኑን መጠየቅ የለብህም” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ድንቅ ነው

ስሙን ለምን መጠየቅ እንደማይኖርባቸው በይበልጥ ግልጽ ማድረጉ ይጠቅም ይሆናል። አ.ት፡ “ለመረዳት እጅግ ያስቸግራችሁ ይሆናል”

Judges 13:19

ከእህል ቁርባኑ ጋር

ይህ ሕግ የሚቃጠል መሥዋዕት በሚቀርብበት ጊዜ የእህል ቁርባን እንዲቀርብ ያዛል። አ.ት፡ “ከእርሱም ጋር የታዘዘውን የእህል ቁርባን” ወይም “አብሮት እንዲሆን የእህል ቁርባን”

በዐለቱ ላይ

“በመሠዊያው ላይ”። ማኑሄ መሥዋዕቱን ያቀረበበት መሠዊያ ዐለት ነበር።

አንድ ነገር አደረገ

“መልአኩ አንድ ነገር አደረገ”

የእግዚአብሔር መልአክ በመሠዊያው ነበልባል ውስጥ ወደ ላይ ወጣ

“የእግዚአብሔር መልአክ በመሠዊያው ነበልባል ውስጥ ተመልሶ ወደ ሰማይ ሄደ”

በፊታቸው በመሬት ላይ ተደፉ

“በግምባራቸው ተደፉ” ይህ የአድናቆትና የአክብሮት ምልክት ነው፣ ሆኖም እግዚአብሔርን መፍራታቸውንም ያሳያል። (ምሳሌአዊ ድርጊት የሚለውን ተመልከት)

Judges 13:21

የእግዚአብሔር መልአክ እንደ ነበረ

“እርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ማኑሄና ሚስቱ ያዩትን ሰው ነው።

እግዚአብሔርን ስላየነው በእርግጥ መሞታችን ነው

እግዚአብሔር እንደሚገድላቸው ማሰባቸውን ያሳያል። ይህ ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ስላየነው ይገድለናል”

Judges 13:23

እነዚህን ነገሮች ሁሉ አያሳየንም ወይም በዚህ ጊዜ እንዲህ ያሉትን ነገሮች እንድንሰማ አያደርገንም ነበር

የማኑሄ ሚስት ስለ አንዱ ነገር ሁለት ጊዜ የምትናገረው አጽንዖት ለመስጠት ነው። እነዚህ ሁለት መግለጫዎች መጣመር ይችላሉ። አ.ት፡ “እንድናደርግ የፈለገውን አይነግረንም ነበር”

Judges 13:24

ሴቲቱ

“የማኑሄ ሚስት”

ወንድ ልጅ ወለደች

ይህ የልጅ መወለድን ያመለክታል። አ.ት፡ “ወንድ ልጅ ወለደች” ወይም “ወንድ ልጅ አገኘች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

አደገ

“ዐዋቂ ሆነ” ወይም “ጎለመሰ”

የእግዚአብሔር መንፈስ ሊያነቃቃው ጀመረ

እዚህ ጋ የእግዚአብሔር መንፈስ ሳምሶንን ማነቃቃቱ በማሰሮ ውስጥ ያለ ምግብ ከሚማሰልበት መንገድ ጋር ተነጻጽሯል። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር መንፈስ በሳምሶን ላይ ተጽዕኖ ማድረግ ጀመረ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ማህነህ ዳን -- ኤሽታኦል

ማህነህ ዳን ለዘለቄታቸው የሚኖሩበትን በሚፈልጉበት ወቅት የዳን ነገድ በጊዜያዊነት የሰፈሩበት ቦታ ስም ነው። ኤሽታኦል የከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ጾርዓ

የዚህን ከተማ ስም በመሳፍንት 13፡2 በተረጎምክበት መልኩ ተርጉመው


Chapter 14

1 ሳምሶንም ወደ ተምና ወረደ፣ በዚያም ከፍልስጥኤማውያን ሴቶች ልጆች አንዲት ሴት አየ፡፡ 2 ከዚያ በተመለሰ ጊዜ፣ ለአባቱና ለእናቱ እንዲህ ሲል ነገራቸው፣ “በተምና ከፍልስጥኤማውያን ሴቶች ልጆች መካከል አንዲት ሴት አየሁ፡፡ ሚስቴ እንድትሆነኝ አሁን እርስዋን አምጡልኝና አጋቡኝ፡፡ 3 ነገር ግን እንዲህ አሉት፣ “ከዘመዶችህ ሴቶች ልጆች ወይም ከሕዝባችን ሁሉ መካከል ሴት የለምን? ካልተገረዙት ከፍልስጥኤማውያን ሚስት ለመውሰድ ትሄሄዳለህን?” ሳምሶንም ለአባቱ እንዲህ አለው፣ “እርስዋን አምጣልኝ፣ እርስዋን ባየኋት ጊዜ ደስ አሰኝታኛለችና፡፡” 4 ነገር ግን አባቱና እናቱ ይህ ነገር የመጣው ከእግዚአብሔር እንደሆነ አላወቁም፣ እርሱ ከፍልስጥኤማውያን ጋር ግጭት ለመፍጠር ይፈልግ ነበርና፡፡ በዚያን ጊዜ ፍልስጥኤማውያን እስራኤልን ይገዙ ነበርና፡፡ 5 ከዚያም ሳምሶን ከአባቱና ከእናቱ ጋር ወደ ተምና ወረዱ፣ እነርሱም በተምና ወዳለው ወደ ወይኑ አትክልት ስፍራ መጡ፡፡ ከዚያም ከአንበሳ ደቦሎች መካከል አንዱ ተነስቶ መጣና በእርሱ ላይ አገሳበት፡፡ 6 የእግዚአብሔር መንፈስ በድንገት በእርሱ ላይ ወረደ፣ ትንሽ የፍየል ጠቦት እንደሚቆራርጥ እንዲሁ አንበሳውን በቀላሉ ቈራረጠው፣ በእጁም ምንም ነገር አልያዘም ነበር፡፡ ነገር ግን ያደረገውን ነገር ለአባቱ ወይም ለእናቱ አልነገራቸውም፡፡ 7 እርሱም ሄደና ከሴቲቱ ጋር ተነጋገረ፣ እርስዋንም ባያት ጊዜ ሳምሶንን ደስ አሰኘችው፡፡ 8 ከጥቂትም ቀን በኋላ ሊያገባት ተመለሰ፣ የአንበሳውንም በድን ያይ ዘንድ ከመንገድ ዘወር አለ፡፡ በአንበሳ በድን ትራፊ ውስጥ የንብ መንጋ ሰፍሮበት ነበር፣ ማርም ነበረበት፡፡ 9 ማሩንም በእጁ ወስዶ መንገድ ለመንገድ እየበላ ሄደ፡፡ ወደ አባቱና ወደ እናቱ በመጣ ጊዜ፣ ለእነርሱም ሰጣቸውና እነርሱም በሉ፡፡ ነገር ግን ማሩን የወሰደው ከአንበሳ በድን ትራፊ ውስጥ እንደ ሆነ አልነገራቸውም፡፡ 10 የሳምሶን አባትም ሴቲቱ ወደ ነበረችበት ወረደ፣ ሳምሶንም በዚያ ግብዣ አደረገ፣ ይህን ማድረግ የወጣት ወንዶች ወግ ነበርና፡፡ 11 የእርስዋ ዘመዶች ባዩት ጊዜ፣ ከእርሱ ጋር ይሆኑ ዘንድ ሌሎች ሠላሳ ጓደኞች አመጡለት፡፡ 12 ሳምሶንም ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ “አሁን እንቆቅልሽ ልንገራችሁ፡፡ ከእናንተ ውስጥ አንዱ ሰው እንቆቅልሹን ማግኘት ቢችልና በሰባቱ የግብዣ ቀኖች ውስጥ መልሱን ቢነግረኝ፣ ሠላሳ የቀጭን በፍታ ቀሚስና ሠላሳ የክት ልብስ እሰጠዋለሁ፡፡ 13 ነገር ግን እናንተ መልሱን ልትነግሩኝ ካልቻላችሁ፣ ሠላሳ የቀጭን በፍታ ቀሚስና ሠላሳ የክት ልብስ ትሰጡኛላችሁ፡፡” እነርሱም እንዲህ አሉት፣ “እንሰማው ዘንድ እንቆቅልሽህን ንገረን፡፡” 14 እርሱም እንዲህ አላቸው፣ “ከበላተኛው ውስጥ መብል ወጣ፤ ከብርቱም ውስጥ ጣፋጭ ወጣ፡፡” ነገር ግን የእርሱ እንግዶች በሦስት ቀን ውስጥ መልሱን ሊያገኙት አልቻሉም፡፡ 15 በአራተኛውም ቀን ለሳምሶን ሚስት እንዲህ አሏት፣ “የእንቈቅልሹን መልስ እንዲነግረን ባልሽን አግባቢልን፣ አለዚያ ግን እንቺንና የአባትሽን ቤት በእሳት እናቃጥላለን፡፡ ወደዚህ የጠራችሁን ድሃ ልታደርጉን ነውን፡፡” 16 የሳምሶን ሚስት በፊቱ ማልቀስ ጀመረች፤ እንዲህም አለችው፣ “ይህን ሁሉ ያደረግኸው እኔን ስለምትጠላኝ ነው! አንተ አትወደኝም፡፡ ከሕዝቤ ውስጥ ለአንዳንዶቹ እንቈቅልሽ ነግረሃቸዋል፣ ነገር ግን መልሱን ለእኔ አልነገርኸኝም፡፡” ሳምሶንም እንዲህ አላት፣ “ወደዚህ ተመልከቺ፣ ለአባቴና ለእናቴ ካልነገርኋቸው፣ ለአንቺ ልነግርሽ ይገባልን?” 17 ግብዣቸው በሚቆይበት በሰባቱም ቀናት ውስጥ በፊቱ አለቀሰች፡፡ መልሱንም በሰባተኛው ቀን ነገራት ምክንቱም እጅግ በጣም አጥብቃ ስለነዘነዘችው ነው፡፡ መልሱንም ለሕዝቧ ዘመዶች ነገረቻቸው፡፡ 18 በሰባተኛው ቀን ፀሐይ ከመግባትዋ በፊት የከተማይቱ ሰዎች እንዲህ አሉት፣ “ከማር የበለጠ የሚጣፍጥ ምንድን ነው? ከአንበሳስ የበለጠ የሚበረታ ምንድን ነው?” ሳምሶንም እንዲህ አላቸው፣ “በጊደሬ ባታርሱ ኖሮ፣ ለእንቈቅልሼ መልስ ባላገኛችሁ ነበር፡፡” 19 በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መንፈስ በድንገት በሳምሶን ላይ በኃይል ወረደ፡፡ ሳምሶንም ወደ አስቀሎና ወረደና ከሕዝቡ መካከል ሠላሳ ሰዎችን ገደለ፡፡ እርሱም የለበሱትን ሁሉ ከገፈፈ በኋላ ልብሳቸውን በሙሉ ወስዶ እንቈቅልሹን ለመለሱለት ሰዎች ሰጣቸው፡፡ እርሱም በጣም ተናደደና ወደ አባቱ ቤት ወጣ፡፡ 20 የሳምሶን ሚስት ግን በጣም ቅርብ ለሆነው ጓደኛው ተሰጠች፡፡



Judges 14:1

ሳምሶን ወደ ተምና ወረደ

“ወረደ” የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የአባቱ ቤት ካለበት ተምና ዝቅ ባለ ስፍራ ስለሚገኝ ነው። ተምና በሶሬቅ ሸለቆ የሚገኝ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ከፍልስጥኤማውያን ሴቶች ልጆች አንዷ

“ሴት ልጅ” የሚለው ቃል ያላገባችን ወጣት ሴት የሚያመለክት የትህትና አገላለጽ ነው። አ.ት፡ “በፍልስጥኤም ሰዎች መካከል አንዲት ያላገባች ሴት” ወይም “ፍልስጥኤማዊት ልጃገረድ”

አሁን ሚስት እንድትሆነኝ አምጡልኝ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ሳምሶን ወላጆቹ የፍስጥኤማዊቷ ሴት ወላጆችን ለጋብቻ እንዲጠይቁለት ግድ እያላቸው ነው። አ.ት፡ “ሚስት እንድትሆነኝ አሁን አጋቡኝ” ወይም “እርሷን እንዳገባት ቅድመ ዝግጅት አድርጉልኝ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 14:3

በዘመዶችህ መካከል ወይም በሕዝባችን ሁሉ ሴት ልጆች መካከል ሴት ስለጠፋች ነው?

ይህንን ጥያቄ ሳምሶንን የሚጠይቁት ከገዛ ሕዝባቸው መካከል ሚስት ሊያገኙለት እንደሚችሉ አሳብ ለመስጠት ነው። ይህ ጥያቄ በመግለጫነት ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “በርግጥ ማግባት እንድትችል በሕዝብህ መካከል ሴቶች አሉ” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

የዘመዶችህ ሴቶች ልጆች

“ሴት ልጅ” የሚለው ቃል ያላገባችን ወጣት ሴት የሚያመለክት የትህትና አገላለጽ ነው። አ.ት፡ “በዘመዶችህ መካከል ካላገቡት ሴቶች አንዷን”

ካልተገረዙት ከፍልስጥኤማውያን ሚስት ልታገባ ነው?

ይህ ጥያቄ የተጠየቀው ሳምሶንን ለመገሰጽ ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊጻፍ ይችላል። ወላጆቹ ፍልስጥኤማዊት እንዲያገባ ያልፈለጉበትን ምክንያት ግልጽ ማድረግ ትችላለህ። አ.ት፡ “የፍልስጥኤም ሰዎች እግዚአብሔርን ስለማያመልኩ በእርግጠኝነት ፍልስጥኤማዊት ማግባት አይኖርብህም”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ እና የሚለውን ተመልከት)

እርሷን አምጡልኝ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። ሳምሶን ስለ ጋብቻው የፍልስጥኤማዊቷን ሴት ወላጆች እንዲያነጋግሩለት ወላጆቹን ግድ እያላቸው ነበር። አ.ት፡ “አሁን ሚስት እንድትሆነኝ አዘጋጁልኝ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ታስደስተኛለች

ይህ ማለት ሴቲቱ ቆንጆ እንደ ሆነች ሳምሶን ያስባል። “ቆንጆ በመሆኗ ደስ ብሎኛል” ወይም “እርሷ ቆንጆ ናት”

ይህ ጉዳይ

ይህ የሚያመለክተው ፍልስጥኤማዊቱን ሴት ለማግባት ሳምሶን ያቀረበውን ጥያቄ ነው።

ግጭት ለመፍጠር ፈልጓልና

“እርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው እግዚአብሔርን ነው።

Judges 14:5

ሳምሶን ወደ ተምና ወረደ

“ወረደ” የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የአባቱ ቤት ካለበት ተምና ዝቅ ባለ ስፍራ ስለሚገኝ ነው። ተምና በሶሬቅ ሸለቆ የሚገኝ ከተማ ነበር። የዚህን ከተማ ስም በመሳፍንት 14፡1 እንዳደረግኸው በተመሳሳይ መንገድ ተርጉመው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እነሆ፣ አንድ የአንበሳ ደቦል መጣበት

እዚህ ጋ “እነሆ” የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የአንባቢዎችን ትኩረት በታሪኩ ውስጥ ወደሚመጣው አስደናቂ ሁነት ለመሳብ ነው። “መጣበት” የሚለው ቃል ትርጉሙ አንበሳው ወደ እርሱ ቀርቧል ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እያገሳበት ነበር

“አስፈራራው”። ይህ አንበሳ አንድን እንስሳ ለማጥቃት በሚያስፈራራበት ጊዜ የሚያሰማው ዓይነት ድምፅ ነው።

የእግዚአብሔር መንፈስ በእርሱ ላይ በድንገት መጣበት

“መጣበት” የሚለው ቃል ትርጉሙ የእግዚአብሔር መንፈስ ሳምሶን ላይ ተጽዕኖ አሳደረበት ማለት ነው። በዚህ ጉዳይ፣ በኃይል አበረታው። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር መንፈስ በኃይል አበረታው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ቆራረጠው

ለሁለት ቆራረጠው

በእጁ ምንም ነገር ሳይኖር

እዚህ ጋ፣ በእጁ ምንም ነገር ሳይኖር የሚለው መግለጫ የጦር መሣሪያ አልያዘም ነበር ለሚለው አጽንዖት ለመስጠት ነው። አ.ት፡ “የጦር መሣሪያ አልነበረውም”

Judges 14:7

ሳምሶንን አስደሰተችው

ይህ ማለት በጣም ቆንጆ እንደሆነች አስቧል። አ.ት፡ “በቁንጅናዋ ተደስቷል” ወይም “በጣም ቆንጆ እንደ ነበረች አስቧል”

ፈቀቅ አለ

ይህ ማለት፣ አንድ ነገር ለማድረግ መንገዱን ትቶ ወጣ አለ። አ.ት፡ “መንገዱን ትቶ ወጣ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሬሳ

የሞተ አካል

እነሆ፣ ንቦች ወረዉት ነበር

እዚህ ጋ “እነሆ” የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የአንባቢዎችን ትኩረት በታሪኩ ውስጥ ወደሚመጣው አስደናቂ ሁነት ለመሳብ ነው። አ.ት፡ “ንቦች ወረዉት አገኘው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

መውረር

እጅግ የበዙ ነፍሳት

አፍሶ

“ሰብስቦ”

Judges 14:10

የሳምሶን አባት ሴቲቱ ወደነበረችበት ወረደ

“ወረደ” የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የሳምሶን አባት ከሚኖርበት ተምና ዝቅ ባለ ስፍራ የሚገኝ መሆኑን ለመግለጽ ነው። አ.ት፡ “የሳምሶን አባት ሴቲቱ ወደምትኖርበት ሄደ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የወጣቶቹ ልማድ

ይህ የጋብቻ ልማድ እንደ ነበረ መግለጹ ጠቃሚ ይሆን ይሆናል። አ.ት፡ “የሚያገቡ ወጣቶች ልማድ”

ሠላሳ ጓደኞቻቸው

“30 ጓደኞቻቸው” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 14:12

ዕንቆቅልሽ

ተጫዋቾቹ ለአስቸጋሪው ጥያቄ መልስ ማግኘት የሚኖርባቸው ውድድር

መፍታት የሚችል

ይህ ማለት የዕንቆቅልሹን ትርጉም መንገር የሚችል ማለት ነው። አ.ት፡ “ትርጉሙን መንገር የሚችል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሠላሳ የላይነን ቀሚስና ሠላሳ ሙሉ ልብስ

“30 የላይነን ቀሚሶችንና 30 ሙሉ ልብስ” (ቁጥሮችን ተመልከት)

ልትነግሩኝ ካልቻላችሁ ግን

እዚህ ጋ “እናንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር ሲሆን የሚያመለክተው በግብዣው ላይ የነበሩትን እንግዶች ነው።

ላይነን

የልብስ ዓይነት

Judges 14:14

ከበላተኛው ውስጥ የሚበላ ነገር

“ከበላተኛው ውስጥ የሚበላ ነገር ተገኘ” ወይም “አንድ የሚበላ ነገር ከአንድ ከሚበላ ነገር ውስጥ ወጣ”

በላተኛው

“በላተኛው” የሚለው ስም ወደ ግሣዊ ሐረግ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሚባላው ነገር”

ከብርቱው ውስጥ የሚጣፍጥ ነገር

“ከብርቱው ውስጥ የሚጣፍጥ ነገር ወጣ” ወይም “ብርቱ ከሆነው ነገር ውስጥ ጣፋጭ የሆነ ነገር ወጣ”

ብርቱው

ይህ የሚያመለክተው ብርቱ የሆነን ነገር ነው። አ.ት፡ “ብርቱው ነገር”

እንግዶቹ

“በግብዣው ላይ የነበሩት ሰዎች”

መልሱን ማግኘት አልቻሉም

እዚህ ጋ፣ የዕንቆቅልሹን መልስ መንገር እንደ አንዳች የተደበቀና እንግዶቹ ፈልገው ሊያገኙት እንደሚያስፈልጋቸው ነገር ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “መልሱን መንገር አልቻሉም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 14:15

አራተኛው ቀን

“ቀን 4”

ማታለል

እነርሱ ሊያደርጉት የማይፈልጉትን ነገር እንዲያደርግ አንድን ሰው ማሳሳት ወይም ማሞኘት

የአባትሽን ቤት

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ይህ ትክክለኛውን ቤት ያመለክታል። አ.ት፡ “አባትሽና ቤተሰቡ የሚኖሩበትን ቤት” ወይም 2) “ቤት” የሚያመለክተው በውስጡ የሚኖሩትን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “ቤተሰብሽ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

እናቃጥለዋለን

“እናቃጥለዋለን” የሚለው ቃል ትርጉም አንድን ነገር ሙሉ በሙሉ ማቃጠል ማለት ነው። አንድ ሰው “ከተቃጠለ” ያ ሰው ተቃጥሎ ሞቷል ማለት ነው።

የጋበዛችሁን ልታደኸዩን ነው?

ክፉ ስለማድረጓ ለመክሰስ ይህንን ይጠይቋታል። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “እዚህ የጠራሽን ድኻ ልታደርጊን ነው!”

ድኻ ልታደርጊን

ዕንቆቅልሹን ካልፈቱና አዲስ ልብሶች ከገዙለት ድኻ ይሆናሉ። አ.ት፡ “አዲስ ልብሶች እንድንገዛለት በማስገደድ ድኻ ልታደርጊን ነው”

Judges 14:16

ፈጽሞ ጠልተኸኛል! አትወደኝም

የሳምሶን ሚስት አጽንዖት ለመስጠት ያህል ሁለት ጊዜ የምትናገረው በመሠረቱ አንድ ነው። አ.ት፡ “በእውነት ፈጽሞ አትወደኝም”

ዕንቆቅልሽ

ተጫዋቾቹ ለአስቸጋሪው ጥያቄ መልስ ማግኘት የሚኖርባቸው ውድድር

ወዲህ ተመልከቱ

ይህ ጥቅም ላይ የዋለው የአንድን ሰው ትኩረት ለማግኘት ነው። እዚህ ጋ “ተመልከቱ” ማለት “አድምጡ” ማለት ነው። አ.ት፡ “አድምጡኝ” ወይም “የምናገረውን ልብ በሉ”

ለአባቴ ወይም ለእናቴ ካልነገርኳቸው ላንቺ መንገር አለብኝ?

መልሱን እንዲነግራት ግድ ስላለችው ሳምሶን እየገሰጻት ነበር። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሆኖ ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “ለአባቴ ወይም ለእናቴ እንኳን አልነገርኳቸውም፤ አልነግርሽም” ወይም “ከአንቺ ይልቅ ቅርቤ ለሆኑት ለወላጆቼ እንኳን አልነገርኳቸውምና እንድነግርሽ ግድ ልትዪኝ አይገባም”

ግብዣቸው በሚቆይባቸው በሰባቱ ቀናት

ሊሆኑ የሚችሉት ትርጉሞች 1) “በግብዣቸው በሰባቱ ቀናት” ወይም 2) “ከሰባቱ የግብዣቸው ቀናት በቀሩት”

ሰባተኛው ቀን

“ቀን 7”

በጣም ነዘነዘችው

እዚህ ጋ “ነዘነዘችው” የሚለው ቃል ትርጉም “ግድ አለችው” የሚል ይሆናል። አ.ት፡ “እንዲነግራት መጨቅጨቋን ቀጠለች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 14:18

የከተማዪቱ ሰዎች

ይህ የሚያመለክተው የሳምሶን ሚስት ዘመዶችን ነው። ይህ በግልጽ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “ወጣቶቹ” ወይም “ዘመዶቿ”

ሰባተኛው ቀን

“ቀን 7”

ከማር ይልቅ የሚጣፍጥ ምንድነው? ከአንበሳስ ይልቅ የሚበረታ ምንድነው?

ይህ የዕንቆቅልሹ መልስ ነው። በጥያቄ ፈንታ እንደ መግለጫ ሆኖ መጻፍ ይኖርበት ይሆናል። አስፈላጊ ከሆነ ተጨማሪ መረጃ በማከል ይህ ከዕንቆቅልሹ ጋር እንዴት እንደሚዛመድ ግልጽ ማድረግ ይቻላል። አ.ት፡ “ማር ጣፋጭ ነው፣ አንበሳም ብርቱ ነው” ወይም “ማር ጣፋጭ ነው፣ እርሱም ከአንበሳ ውስጥ ወጣ” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ እና የሚለውን ተመልከት)

በጥጃዬ ባታርሱ ኖሮ

ሳምሶን መልሱን ለማግኘት ሚስቱን መጠቀማቸውን አንድ ሰው የራሱን እርሻ ለማረስ የሌላውን ሰው ጥጃ ከመጠቀሙ ጋር ያነጻጽራል። አ.ት፡ “በሚስቴ ባትጠቀሙ ኖሮ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ማረስ

ማረስ ማለት ዐፈሩን ለዘር ለማዘጋጀት እንስሳን በመጠቀም ስለታማውን ብረት ዐፈር ውስጥ አስገብቶ መሳብ ነው።

Judges 14:19

በሳምሶን ላይ በኃይል መጣበት

“መጣበት” የሚለው ቃል ትርጉሙ የእግዚአብሔር መንፈስ ሳምሶን ላይ ተጽዕኖ አሳደረበት ማለት ነው። በዚህ ጉዳይ፣ በኃይል አበረታው። አ.ት፡ “የእግዚአብሔር መንፈስ በኃይል አበረታው” ወይም “ሳምሶንን በጣም ኃይለኛ አደረገው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከሰዎቻቸው ሠላሳውን ገደለ

“ከሰዎቻቸው 30 ገደለ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ከሰዎቻቸው

በዚያ የሚኖሩትን ሰዎች”

ብዝበዛ

አብዛኛውን ጊዜ ከውጊያ ወይም ከጦርነት በኋላ በኃይል የሚወሰዱ ነገሮች

ልብሶቻቸውን

እነዚህ ከአስቀሎና የወሰዳቸው ብዝበዛዎቹ ነበሩ። አ.ት፡ “የወሰዳቸውን ሙሉ ልብሶች”

በቁጣ ነዶ

“በጣም ተናዶ”

ወደ አባቱ ቤት ወጣ

እዚህ ጋ የአባቱ ቤት ከሚገኝበት አካባቢ ሳምሶን የነበረበት ተምና የመሬት አቀማመጡ ዝቅ ያለ ስለነበረ “ወጣ” የሚለው ቃል ጥቅም ላይ ውሏል።

የሳምሶን ሚስት ለቅርብ ጓደኛው ተሰጠች

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሚስቱ አባት እርሷን ለቅርብ ጓደኛው ሰጣት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

የቅርብ ጓደኛ

“ከሌላው የቀረበ ጓደኛ”


Chapter 15

1 ከጥቂት ቀናትም በኋላ በስንዴ መከር ጊዜ፣ ሳምሶን የፍየል ጠቦት ይዞ ሚስቱን ሊጠይቅ ሄደ፡፡ ለራሱም እንዲህ አለ፣ “ወደ ሚስቴ ወደ ጫጉላው ቤት ልግባ፡፡” ነገር ግን አባትዋ ወደ ውስጥ እንዳይገባ ከለከለው፡፡ 2 አባትዋም እንዲህ አለ፣ “እኔ በእርግጠኝነት የጠላሃት መሰለኝ፣ ስለዚህም ለጓደኛህ ሰጠኋት፡፡የእርስዋ ታናሽ እኅት ከርስዋ የበለጠች ቆንጆ ናት፣ አይደለችም እንዴ? በእርስዋ ፋንታ ታናሽዋን ውሰዳት፡፡” 3 ሳምሶንም ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ “ከእንግዲህ ወዲህ በፍልስጥኤማውያን ላይ ጉዳት ባደረስሁባቸው ጊዜ እኔ ንጹሕ ነኝ፡፡” 4 ሳምሶንም ሄደና ሦስት መቶ ቀበሮዎች ያዘ፣ ሁለት ሁለቱንም ቀበሮዎች በአንድ ላይ በጅራታቸው አሰራቸው፡፡ ከዚያም ችቦዎችን ወስዶ በእያንዳንዱ ጥንድ በሁለቱም ጅራቶች መካከል አሰራቸው፡፡ 5 ችቦውንም በእሳት ባቀጣጠለው ጊዜ፣ ቀበሮዎቹን በቆመው በፍልስጥኤማውያን እህል መካከል እንዲሄዱ አደረጋቸው፣ የእህሉን ነዶና በእርሻ ውስጥ የቆመውንም እህል፣ ከወይኑ አትክልት ስፍራና ከወይራውም ተክል ጋር አቃጠሉት፡፡ 6 ፍልስጥኤማውያንም እንዲህ በማለት ጠየቁ፣ “ይህን ያደረገው ማን ነው?” እነርሱም “ይህን ያደረገው የተምናዊው አማች ሳምሶን ነው፣ ምክንያቱም ተምናዊው የሳምሶንን ሚስት ወስዶ ለጓደኛው ሰጥቶአታልና” አሉ፡፡ ፍልስጥኤማያንም ሄደው እርስዋንና አባትዋን በእሳት አቃጠሉ፡፡ 7 ሳምሶንም “እናንተ ይህንን ካደረጋችሁ፣ እኔ እበቀላችኋለሁ፣ እኔ የማርፈው ይህን ካደረግሁ በኋላ ነው” አላቸው፡፡ 8 እርሱም ዳሌአቸውንና ጭናቸውን ቆራረጣቸውና በታላቅ አገዳደል ገደላቸው፡፡ ከዚያም ወርዶ በኤጣም ዓለት ባለው ዋሻ ውስጥ ተቀመጠ፡፡ 9 የዚያን ጊዜ ፍልስጥኤማውያን ወጡና በይሁዳ ጦርነት ለማካሄድ ተዘጋጁ፣ ሰራዊታቸውንም በሌሒ ውስጥ አሰፈሩ፡፡ 10 የይሁዳም ሰዎች እንዲህ አሉ፣ “እኛን ለመውጋት የመጣችሁት ለምንድን ነው?” እነርሱም እንዲህ አሉ፣ “የምንወጋችሁ ሳምሶንን ለመያዝ ነው፣ እርሱ በእኛ ላይ እንዳደረገው እኛም በእርሱ ላይ ልናደርግበት ነው፡፡” 11 ሦስት ሺህ የይሁዳ ሰዎችም በኤጣም ዓለት ወዳለው ዋሻ ወረዱና፣ ለሳምሶን እንዲህ አሉት፣ “ፍልስጥኤማውያን በእኛ ላይ ገዢዎች እንደሆኑ አታውቅምን? ይህ በእኛ ላይ ያደረግኸው ነገር ምንድን ነው?” ሳምሶንም ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ “እነርሱ በእኔ ላይ አደረጉብኝ፣ እኔም በእነርሱ ላይ አደረግሁባቸው፡፡” 12 እነርሱም ለሳምሶን እንዲህ አሉት፣ “አንተን አስረን ለፍልስጥኤማውያን እጅ አሳልፈን ልንሰጥህ መጥተናል፡፡” ሳምሶንም እንዲህ አላቸው፣ “እናንተ ራሳችሁ እንደማትገድሉኝ ማሉልኝ፡፡” 13 እነርሱም እንዲህ አሉት፣ “አንገድልህም፣ በገመድ አስረን ብቻ ለእነርሱ አሳልፈን እንሰጥሃለን፡፡ እንደማንገድልህ ቃል እንገባልሃለን፡፡” ከዚያም በሁለት አዲስ ገመዶች አሰሩትና ከዓለቱ ውስጥ አወጡት፡፡ 14 ወደ ሌሒ በመጣ ጊዜ፣ ፍልስጥኤማውያን እየጮሁ መጡ፣ አገኙትም፡፡ የዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መንፈስ በእርሱ ላይ በኃይል ወረደበት፡፡ ክንዶቹ የታሰሩበት ገመዶችም በእሳት እንደ ተቃጠለ የተልባ እግር ፈትል ከእጆቹ ላይ ወደቁ፡፡ 15 ሳምሶንም አዲስ የአህያ መንጋጋ አገኘ፣ እጁንም ዘርግቶ አነሳውና በእርሱ አንድ ሺህ ሰዎች ገደለ፡፡ 16 ሳምሶንም እንዲህ አለ፣ “በአህያ መንጋጋ ክምር በክምር ላይ አድርጌአቸዋለሁ፣ በአህያ መንጋጋ አንድ ሺህ ሰዎች ገድያለሁ፡፡” 17 ሳምሶንም መናገሩን በፈጸመ ጊዜ፣ የአህያ መንጋጋውን ከእጁ ጣለው፣ ያም ስፍራ ራማትሌሒ ተብሎ ተጠራ፡፡ 18 ሳምሶን በጣም ተጠምቶ ነበርና ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ጮኸ፣ “አንተ ይህን ታላቅ ድል ለአገልጋይህ ሰጥተሃል፣ ነገር ግን አሁን በጥም እሞታለሁ፣ ባልተገረዙትም ሰዎች እጅ እወድቃለሁ፡፡” 19 እግዚአብሔርም በሌሒ ያለውን ክፍት ስፍራ ሰንጥቆ ከፈተው፣ ከእርሱም ውኃ ወጣ፡፡እርሱም በጠጣ ጊዜ፣ ብርታቱ ተመለሰና ተጠናከረ፡፡ ስለዚህ የዚያ ቦታ ስም ዓይንሀቆሬ ተብሎ ተጠራ፣ እስከ ዛሬ ድረስ በሌሒ ይገኛል፡፡ 20 ሳምሶን በፍልስጥኤማውያን ዘመን በእስራኤል ላይ ለሀያ ዓመት ፈረደ፡፡



Judges 15:1

ራሱን ጠየቀ

ይህ ማሰብን ያመለክታል። አ.ት፡ “በራሱ አሰበ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ወደ ሚስቴ ክፍል እሄዳለሁ

ሳምሶን ከሚስቱ ጋር ለመተኛት አስቦ ነበር። ይህ በግልፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አብረን እንድንተኛ ወደ ሚስቴ ክፍል አሄዳለሁ”

እንዲገባ አልፈቀደለትም

ሳምሶን ለራሱ ከተናገረው ውስጥ “የእርሷ ክፍል” የሚለውን ሐረግ መረዳት ይቻላል። ይህ እዚህ ጋር መደገም ይችላል። አ.ት፡ “ወደ ክፍሏ እንዲገባ አልፈቀደለትም”

ስለዚህ ለጓደኛህ ሰጠኋት

ይህ ማለት ሚስት እንድትሆነው ለጓደኛው ሰጣት ማለት ነው። ይህ በግልፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከእርሱ ጋር እንድትጋባ ለጓደኛህ ሰጠኋት”

አይደለችምን?

ይህን ጥያቄ የሚጠይቀው ሳምሶን ከእርሱ ጋር ሊስማማ እንደሚገባ ለማመልከት ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “እንደምትስማማ ተስፋ አደርጋለው”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

በምትኳ ውሰዳት

ሳምሶን እንደ ሚስቱ እንዲወስዳት አስተያየት እየሰጠ ነው። ይህ በግልፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በእርሷ ምትክ ሚስት እንድትሆንህ ውሰዳት”

Judges 15:3

ፍልስጥኤማውያንን በምጎዳቸው ጊዜ ንጹሕ እሆናለሁ

ሳምሶን፣ ፍልስጤማውያን ስለበደሉት ቢያጠቃቸው ንጹሕ እንደሚሆን ያስባል። ይህ በግልፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስለበደሉኝ ፍልስጤማውያንን ብጎዳቸው ንጹሕ እሆናለሁ”

ሦስት መቶ ቀበርዎች

“300 ቀበርዎች”

ቀበሮዎች

ቀበሮዎች እንደ ውሻ ያሉ ረጃጅም ጭራ ያላቸው፣ በጎጆ የሚኖሩ ወፎችንና ሌሎች ትናንሽ እንስሶችን የሚመገቡ እንስሶች ናቸው።

እያንዳንዱ ጥንድ

ጥንድ ማለት የትኛውም ነገር ሁለት ሆኖ ሲገኝ ነው፤ እንደ ሁለት ቀበርዎች ወይም ሁለት ጭራዎች።

ጭራ ከጭራ ጋር

“በጭራዎቻቸው”

ችቦዎች

ችቦ በአንደኛው ጫፉ ተቀጣጣይ ነገር የተደረገበት የእንጨት ጭራሮ ነው፤ ችቦ በአብዛኛው ሊሎች ነገሮችን ለመለኮስ ወይም ብርሃን እንዲሰጥ የሚያዝ ነው።

Judges 15:5

የቆመ እህል

በእርሻ ውስጥ ገና በአገዳው ላይ እያደገ ያለ እህል

የተከመረ እህል

ከታጨደ በኋላ ተሰብስበው የተከመሩ የእህል ነዶዎች

ተክሎች

የፍራፍሬ ዛፎች የሚበቅሉበት ቦታ ነው።

የተምናዊው አማች

የአንድ ሰው የሴት ልጁ ባል ለሰውየው “አማች” ነው።

ተምናዊው

ይህ ከተምናህ የሆነ ሰው ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የሳምሶንን ሚስት ወስዶ ለጓደኛው ሰጠው

የሳምሶን ሚስት አባት እርሷን የሳምሶን ጓደኛ እንዲያገባት ሰጠው። ይህ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሳምሶንን ሚስት ወስዶ የሳምሶንን ጓደኛ እንድታገባው ፈቀደላት”

ፈፅመው አቃጠሏቸው

“ፈፅመው አቃጠሏቸው” የሚለው ሐረግ አንድን ነገር ጨርሶ ማቃጠል ማለት ነው። አንድ ሰው “ፈፅሞ ተቃጠለ” ማለት ያ ሰው ተቃጥሎ ሞተ ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 15:7

እነርሱን አላቸው

“ፍልስጤማውያኑን አላቸው”

እናንተ ይህንን ካደረጋችሁ

“ይህንን ስላደረጋችሁ”

ሽንጥና ታፋቸውን ቆራረጣቸው

እዚህ ጋ “ሽንጥና ታፋ” ሙሉ ሰውነትን ያመለክታል። ይህ ሳምሶን ፍልስጥኤማውያንን እንዴት እንደገደላቸው የሚያሳይ ጉልህ ገለጻ ነው። አ.ት፡ “ሰውነታቸውን ቆራረጠው”።

ወደ ታች ወረደ

እዚህ ጋ “ወደታች ወረደ” የሚለው ሐረግ ከከፍታ መውረዱን ማመልከቱ ላይሆን ይችላል፤ እንዲያውም አንድ ሰው ወደ ሌላ ቦታ መጓዙን መግለጫ መንገድ ነው። አ.ት፡ “ሄደ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ዋሻ

በኮረብታ ወይም ተራራ ውስጥ ያለ ክፍት ቦታ

ገደል

ከፍ ያለ ዐለታማ ኮረብታ ወይም የተራራ ጎን

ኢታም

ይህ በኢየሩሳሌም አቅራቢያ ያለ የዐለታማ ኮረብታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 15:9

በይሁዳ - ፍልስጥኤማውያኑ ወደ ላይ ወጡ …

እዚህ ጋ “ወደ ላይ ወጡ” የሚለው ሐረግ ጥቅም ላይ የዋለው ፍልስጥኤማውያኑ እነርሱ ይጓዙበት ከነበሩበት ቦታ በከፍታ ወደሚበልጠው ይሁዳ ስለመጡ ነው።

ለጦርነት ተዘጋጅተው

“ራሳቸውን ለጦርነት አዘጋጅተው”

ሌሒ

ይህ በይሁዳ ያለ ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ እንዳደረገብን ልናደርግበት ነው

ፍልስጥኤማውያኑ ሳምሶን ብዙዎቹን ፍልስጥኤማውያን እንደገደለ እንዴት እንደሚገሉት እያነጻጸሩ ነው። አ.ት፡ “ብዙ ሰዎቻችንን እንደገደለ ግደሉት”

Judges 15:11

የይሁዳ ሶስት ሺህ ወንዶች

“3000 የይሁዳ ወንዶች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በኢታም ገደል ያለ ዋሻ

ይህንን ሐረግ በመሳፍንት 15፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ፍልስጥኤማውያን በእኛ ላይ ገዢዎች እንደሆኑ አታውቅም? በእኛ ላይ ያደረከው ይህ ምንድን ነው?

የይሁዳ ሰዎች እነዚህን ጥያቄዎች የሚጠይቁት ሳምሶንን ለመገሰጽ ነው። እነዚህ ጥያቄዎች እንደ መግለጫ ሊጻፉ ይችሉ ይሆናል። አ.ት፡ “ፍልስጤማውያን በኛ ላይ ገዢዎች እንደሆኑ ታውቃለህ ነገር ግን አንተ የምታደርገው እንዳልሆኑ ያህል ነው። ያደረከው ነገር ከባድ ጉዳት አምጥቶብናል።” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አደረጉብኝ፥ ስለዚህ እኔም አደረግሁባቸው

ሳምሶን ሚስቱን እንዴት እንደገደሉበትና እርሱ በበቀል እንዴት እንደገደላቸው እያመለከተ ነው። ይህ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሚስቴን ገድለዋታል፤ ስለዚህ እኔም ገደልኳቸው።”

Judges 15:12

የፍልስጥኤማውያን እጅ

እዚህ ጋ “እጅ” የሚያመለክተው ኃይልን ነው። አ.ት፡ “የፍልስጥኤማውያኑ መቆጣጠር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በእጃቸው አሳልፈን ልንሰጥህ

ይህ ማለት አንድን ሰው በሌላ ሰው ቁጥጥር ስር እንዲሆን ማድረግ ማለት ነው። አ.ት፡ “ለፍልስጥኤማውያኑ ልንሰጥህ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ከዐለቱ ወደላይ

ይህ ሳምሶን በመሳፍንት 15፡8 ላይ ሄዶበት የነበረውን በኢታም ገደል የሚገኘውን ዋሻ ያመለክታል። እዚህ ጋ “ወደ ላይ” የሚለው ቃል ከዋሻው አውጥተው አምጥተውታል ማለት ነው። አ.ት፡ “በትልቁ ዐለት ውስጥ ካለው ዋሻ አውጥተው”።

Judges 15:14

በመጣ ጊዜ

ሳምሶን ብቻውን እልተጓዘም፤ በገመድ ባሰሩት ሰዎች እየተመራ ነበር። አ.ት፡ “በመጡ ጊዜ”

ሌሒ

ይህ በይሁዳ የሚገኝ ከተማ ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 15፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

በእርሱ ላይ በኃይል መጣበት

“በላዩ ላይ መጣበት” የሚለው ሐረግ የእግዚአብሔር መንፈስ ሳምሶን ላይ ተጽዕኖ አሳድሯል ማለት ነው። በዚህ ቦታ፤ በጣም ብርቱ አድርጎታል። አ.ት፡ “ሳምሶንን በጣም ብርቱ አደረገው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በክንዱ ላይ የነበሩት ገመዶች እንደ ተቃጠለ ፈትል ሆኑ

ሳምሶን እጁ የታሰረበትን ገመድ በቀላሉ በጣጥሶታል። ደራሲው ገመዱን እንዴት በቀላሉ እንደበጣጠሰው ለመግለጽ እንደተቃጠለ ፈትል ይለዋል። አ.ት፡ ”በክንዱ ላይ ያሉትን ገመዶች ፈትል በቀላሉ እንደሚቃጠል በጣጠሳቸው”

የተልባ ፈትል

ከተልባ ተክል የሚገኝ ቃጫና ክር ጨርቅ ለመስራት ይጠቅማል።

Judges 15:15

አዲስ መንጋጋ

ይህ ማለት አህያው በቅርብ የሞተና አጥንቶቹም ገና መበስበስ ያልጀመሩ ናቸው ማለት ነው። መንጋጋ የታችኛዎቹን ጥርሶች የሚይዝ አጥንት ነው።

አንድ ሺህ ሰዎች

“1000 ወንዶች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የአህያው መንጋጋ

“የአህያ መንጋጋ”

ክምር በክምር

ይህ ሐረግ ሳምሶን ምን ያህል ሰዎችን እንደገደለ ይገልጻል። ትልቅ የሬሳ ክምር ለመሥራት የሚበቃ ሬሳ ነበር። አ.ት፡ “ሬሳዎች ከምሬአለሁ”

Judges 15:17

ራማት ሌሒ

ይህ የቦታ ስም ነው። ስሙም “የመንጋጋ ኮረብታ” ማለት ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

በጣም ተጠምቶ ነበር

“ውሃ መጠጣት በጣም አስፈለገው”

ነገር ግን አሁን በውሃ ጥም ሞቼ ባልተገረዙት. . . እወድቃለሁ?

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) ሳምሶን በጣም ከመጠማቱ የተነሳ የምር ሊሞት እንደሆነ። አ.ት፡ “ነገር ግን አሁን በጥም እሞታለሁ፣ ሰውነቴም ባልተገረዙት … ይወድቃል”። ወይም 2) ሳምሶን በጥም ይሞት እንደሆነ በመጠየቅ ምን ያህል እንደተጠማ ያጋንናል። አ.ት፡ “ነገር ግን አሁን በጥሜ ምክንያት እንድደክም፤ ባልተገረዙትም … እንድወድቅ ትፈቅዳለህ?” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

በጥም መሞት

ይህ ማለት በቂ ውሃ ባለመጠጣትህ ምክንያት በሰውነትህ ውስጥ በቂ ውሃ አጥተህ መሞት ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በእነዚያ ባልተገረዙት እጅ መውደቅ

“በእጃቸው መውደቅ” የሚለው ሐረግ መማረክ ማለት ነው። “እነዚያ ያልተገረዙ” የሚለው ፍልስጤማውያንን ሲሆን “ያልተገረዘ” የሚለው ቃል እግዚአብሔርን የማያመልኩ ስለመሆናቸው አጽንዖት የሚሰጥ ቃል ነው። አ.ት፡ “እግዚአብሔርን በማያውቁ ፍልስጥኤማውያን መማረክ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 15:19

ተሰንጥቆ ጉድጓድ ተከፈተ

“መሬት ላይ ቀዳዳ ተከፈተ” ወይም “ዝቅ ያለው ስፍራ ተከፈተ”። ይህ የሚያመለክተው እግዚአብሔር ምንጭ እንዲፈልቅ ያደረገበትን ዝቅ ያለ ስፍራ ነው።

ሌሔ

ይህንን በመስፍንት 15፡9 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

ብርታቱ ተመለሰለትና ተነቃቃ

እነዚህ ሁለት ሐረጎች በመሠረቱ የሚናገሩት ስለ አንድ ነገር ሲሆን ሳምሶን እንደገና ስለ መበርታቱ አጽንዖት የሚሰጡ ናቸው። እነዚህ ሁለት መግለጫዎች መጣመር ይችላሉ። አ.ት፡ “እንደገና በረታ” ወይም “ተነቃቃ”

ዓይንሀቆሬ

ይህ የውሃ ምንጭ ስም ነው። ስሙ “የጸለየው የእርሱ ምንጭ” ማለት ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

እስካሁን ድረስ በሌሒ ይገኛል

ይህ ማለት ምንጩ ሳይደርቅ ቆይቷል ማለት ነው። “እስካሁን ድረስ” የሚለው ሐረግ የሚያመለክተው የ”አሁን ጊዜ”ን ነው። አ.ት፡ ዛሬም እንኳን ምንጩ በሌሒ ይገኛል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በፍልስጥኤማውያኑ ዘመን

ይህ ፍልስጥኤማውያን የእስራኤልን ምድር ይቆጣጠሩ የነበረበትን ወቅት ያመለክታል። አ.ት፡ “ፍልስጥኤማውያን እስራኤልን ይገዙ በነበረበት ጊዜ”

ለሃያ አመታት

“ለ 20 ዓመታት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)


Chapter 16

1 ሳምሶን ወደ ጋዛ ሄደና በዚያ ዝሙት አዳሪ ሴት አየ፣ ከእርስዋም ጋር ወደ አልጋ ሄደ፡፡ 2 የጋዛ ሰዎችም “ሳምሶን ወደዚህ መጥቶአል” የሚል ወሬ ሰሙ፡፡ የጋዛ ሰዎች ስፍራውን ከበቡትና ሌሊቱን ሁሉ ተደብቀው በከተማይቱ በር ጠበቁት፡፡ ሌሊቱን ሁሉ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ አላደረጉም፡፡ እንዲህ ብለዋልና፣ “እስኪነጋ ድረስ እንጠብቀው፣ ከዚያም እንገድለዋለን፡፡” 3 ሳምሶንም እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ በአልጋ ላይ ተኛ፡፡ እኩለ ሌሊትም በሆነ ጊዜ ተነሳና የከተማይቱን በር መዝጊያና ሁለቱን መቃኖች ያዘ፡፡ እነርሱንም ከመወርወሪያው ጋር ከመሬት ነቀላቸው፣ በትከሻውም ላይ አደረጋቸው፣ በኬብሮንም ፊት ለፊት ወዳለው ኮረብታ ራስ ላይ ተሸክሞት ወጣ፡፡ 4 ከዚህ በኋላ ሳምሶን በሶሬቅ ሸለቆ የምትኖር አንዲት ሴት ወደደ፡፡ ስምዋም ደሊላ ይባል ነበር፡፡ 5 የፍልስጥኤማውያንም አለቆች ወደ እርስዋ መጡና እንዲህ አሏት፣ “እርሱን ለማዋረድ እናስረው ዘንድ በእርሱ ያለው ታላቅ ኃይል የት እንደሆነና በምን መንገድ እርሱን ማሸነፍ እንደምንችል እንዲያሳይሽ ሳምሶንን አባብዪው፡፡ ይህንን አድርጊልን፣ እኛም እያንዳንዳችን 1, 100 ብር እንሰጥሻለን፡፡ 6 ደሊላም ለሳምሶን እንዲህ አለችው፣ “እባክህ፣ እንዲህ በጣም ብርቱ የሆንከው እንዴት እንደሆነ ንገረኝ፣ በቁጥጥር ስር መዋል እንድትችል ሰው ሊያስርህ የሚችለው እንዴት ነው? 7 ሳምሶንም እንዲህ አላት፣ “ባልደረቁ ሰባት እርጥብ ጠፍሮች ቢያስሩኝ፣ እደክማለሁ፣ እንደ ማንኛውም ሰውም እሆናለሁ፡፡” 8 የፍልስጥኤማውያን አለቆችም ያልደረቁ ሰባት እርጥብ ጠፍሮች አመጡላት፣ እርስዋም ሳምሶንን በእነርሱ አሰረችው፡፡ 9 በዚህን ጊዜ በጓዳዋ ውስጥ ሰዎች በምስጢር ተደብቀው ይጠብቁ ነበር፡፡ እርስዋም፣ “ሳምሶን፣ ፍልስጥኤማውያን መጡብህ” አለችው፡፡ ነገር ግን የተልባ እግር ፈትል እሳት በነካው ጊዜ እንደሚበጣጠስ ጠፍሩን በጣጠሰው፡፡ እነርሱም የብርታቱ ምስጢር ምን እንደሆነ አላወቁም፡፡ 10 ከዚያም ደሊላ ሳምሶንን እንዲህ አለችው፣ “አንተ እኔን እንዴት እንዳታለልኸኝ ግልጽ ሆኗል፣ ሐሰትንም ነገርኸኝ፡፡ እባክህ፣ እንዴት እንደምትታሰር ንገረኝ፡፡” 11 እርሱም እንዲህ አላት፣ “ለሥራ ጥቅም ላይ ፈጽሞ ባልዋሉ በአዲስ ገመዶች ቢያስሩኝ፣ እደክማለሁ፣ እንደ ማንኛውም ሰው እሆናለሁ፡፡” 12 ስለዚህ ደሊላ አዲስ ገመዶች ወሰደችና በእነርሱ አሰረችው፣ እንዲህም አለችው፣ “ሳምሶን፣ ፍልስጥኤማውያን መጡብህ፡፡” ተደብቀው ሲጠብቁ የነበሩት ሰዎች በጓዳዋ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ሳምሶን ገመዶቹን እንደ ፈትል ክር ከክንዶቹ በጣጠሰው፡፡ 13 ደሊላም ሳምሶንን እንዲህ አለችው፣ “እስከ አሁን ድረስ አታልለኸኛልና የነገርኸኝም ውሸት ነው፡፡ አንተን ማሰር የሚቻለው እንዴት እንደሆነ ንገረኝ፡፡” ሳምሶንም እንዲህ አላት፣ “የራሴን ጠጕር ሰባቱን ጕንጕን ከድር ጋር ጎንጉነሽ በችካል ብትቸክዪው፣ እንደ ሌላ ሰው እሆናለሁ፡፡” 14 እርሱም በተኛ ጊዜ፣ ደሊላ የራሱን ጠጕር ሰባቱን ጕንጕን ከድሩ ጋር ጐነጐነችው፣ በችካልም ቸከለችውና፣ እንዲህ አለችው፣ “ሳምሶን፣ ፍልስጥኤማውያን መጡብህ!” እርሱም ከእንቅልፉ ነቃና ችካሉን ከነቆንዳላውና ከነድሩ ነቀለው፡፡ 15 እርስዋም እንዲህ አለችው፣ “ምስጢርህን ለእኔ ሳትነግረኝ ‘እወድሻለሁ’ ልትለኝ እንዴት ትችላለህ? ሦስት ጊዜ ቀለድህብኝ፣ እንዲህ ዓይነቱን ታላቅ ኃይል እንዴት ሊኖርህ እንደቻለ አልነገርኸኝም፡፡” 16 ሞት እስኪመኝ ድረስ ዕለት ዕለት በቃሎችዋ እጅግ በጣም ጨቀጨቀችው፣ ከመጠን በላይም ጫና አደረገችበት፡፡ 17 ስለዚህ ሳምሶን ሁሉንም ነገር ነገራትና እንዲህ አላት፣ “ከእናቴ ማኅፀን ጀምሬ ለእግዚአብሔር ናዝራዊ ሆኜ ስለተለየሁ በራሴ ላይ ምላጭ ደርሶና ጸጉሬን ተላጭቼ አላውቅም፡፡ የራሴን ጸጕር ብላጭ ኃይሌ ከእኔ ይሄዳል፣ እደክማለሁም እንደ ማንኛውም ሰው እሆናለሁ፡፡” 18 ደሊላም ስለ ሁሉ ነገር እውነቱን እንደነገራት ባየች ጊዜ፣ ሰዎች ላከችና የፍልስጥኤማውያንን አለቆች ጠራች፣ እንዲህም አለቻቸው፣ “ሁሉንም ነገር ነግሮኛልና እንደገና ኑ፡፡” የዚያን ጊዜ የፍልስጥኤማውያን አለቆች ብሩን በእጃቸው ይዘው ወደ እርስዋ ሄዱ፡፡ 19 እርስዋም በጭኗ ላይ እንዲተኛ አደረገችው፡፡ ሰባቱን የራሱን ጕንጕን እንዲላጨው አንድ ሰው ጠራች፣ ኃይሉ ስለተለየው እርስዋ በቁጥጥሯ ስር ልታደርገው ጀመረች፡፡ 20 እርስዋም፣ “ሳምሶን፣ ፍልስጥኤማውያን መጡብህ!” አለችው፡፡ እርሱም ከእንቅልፉ ነቅቶ እንዲህ አለ፣ “እንደ ሌላው ጊዜ እወጣለሁ፣ ራሴንም ነጻ አወጣለሁ፡፡” ነገር ግን እግዚአብሔር እንደ ተወው አላወቀም፡፡ 21 ፍልስጥኤማውያንም ያዙትና ዓይኖቹን አወጡት፡፡ ወደ ጋዛም ወሰዱትና በናስ ሰንሰለት አሰሩት፡፡ በእስር ቤትም ውስጥ ሆኖ እህል ይፈጭ ነበር፡፡ 22 ነገር ግን ከተላጨ በኋላ የራሱ ጠጕር እንደገና ያድግ ጀመር፡፡ 23 የፍልስጥኤማውያንም አለቆች ለአምላካቸው ለዳጎን ታላቅ መሥዋዕት ያቀርቡ ዘንድ፣ ደስም ይላቸው ዘንድ በአንድ ላይ ተሰበሰቡ፡፡ እነርሱ “አምላካችን ጠላታችንን ሳምሶንን አሸንፏል፣ በእጃችን አሳልፎ ሰጥቶናል” ብለዋልና፡፡ 24 ሕዝቡም እርሱን ባዩት ጊዜ አምላካቸውን አመሰገኑ፣ እንዲህ ብለዋልና፣ “አገራችንን ያጠፋውን፣ ከእኛም ብዙ ሰው የገደለውን ጠላታችንን አምላካችን አሸነፈው፣ በእጃችንም አሳልፎ ሰጠው፡፡” 25 እጅግ ደስ ባላቸው ጊዜ፣ እንዲህ አሉ፣ “እንዲያስቀን ሳምሶንን ጥሩት፡፡” ሳምሶንን ከእስር ቤት ጠሩትና እንዲስቁ አደረጋቸው፡፡ በምሰሶና በምሰሶ መካከል እንዲቆም አደረጉት፡፡ 26 ሳምሶንም እጁን የያዘውን ልጅ፣ “እደገፍባቸው ዘንድ ሕንጻውን የደገፉትን ምሰሶዎች እንድነካቸው አስጠጋኝ” አለው፡፡ 27 በዚያን ጊዜ ቤቱ በወንዶችና በሴቶች ተሞልቶ ነበር፡፡ የፍልስጥኤም አለቆች ሁሉ በዚያ ነበሩ፡፡ ሳምሶን እነርሱን ሲያዝናናቸው ይመለከቱ የነበሩ ሦስት ሺህ የሚያህሉ ወንዶችና ሴቶች በጣራው ላይ ነበሩ፡፡ 28 ሳምሶንም ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ሲል ጮኸ፣ “ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፣ እንደገና አስበኝ! አምላኬ ሆይ፣ ሁለት ዓይኖቼን ስላወጡ ፍልስጥኤማውያንን አሁን በአንድ ምት እንድበቀል፣ እባክህ፣ ይህን አንድ ጊዜ ብቻ አበርታኝ፡፡” 29 ሳምሶንም ሕንጻው ተደግፎባቸው የነበሩትን ሁለቱን መካከለኞች ምሰሶዎች ጠምጥሞ ያዘ፣ አንዱን ምሰሶ በቀኝ እጁ ሌላውን ደግሞ በግራ እጁ ይዞ በእነርሱ ላይ ተደገፈ፡፡ 30 ሳምሶንም እንዲህ አለ፣ “ከፍልስጥኤማውያን ጋር ልሙት!” በሙሉ ኃይሉ ገፋው፣ ሕንጻውም በውስጡ በነበሩት አለቆችና በሕዝቡም ሁሉ ላይ ወደቀ፡፡ ስለዚህ እርሱ በሞተ ጊዜ የገደላቸው ሰዎች በሕይወት ሳለ ከገደላቸው ይልቅ የበለጡ ነበሩ፡፡ 31 የዚያን ጊዜ ወንድሞቹና የአባቱ ቤተ ሰቦች በሙሉ ወረዱ፣ እርሱንም ይዘው ወሰዱት፣ መልሰው አመጡትና በጾርዓና በኤሽታኦል መካከል ባለው በአባቱ በማኑሄ መቃብር ውስጥ ቀበሩት፡፡ ሳምሶን በእስራኤል ላይ ለሀያ ዓመት ፈረደ፡፡



Judges 16:1

ከእርሷ ጋር ወደ አልጋ ሄደ

“ወደ አልጋ ሄዱ” የሚለው ሐረግ የግብረ ሥጋ ግንኙነት ማድረግን የሚያመለክት የጨዋ አነጋገር ነው። አ.ት፡ “ከእርሷ ጋር የግብረ ሥጋ ግንኙነት አደረገ” ወይም “ከእርሷ ጋር ተኛ”

ለጋዛ ሰዎች ተነግሯቸው ነበር

“የጋዛ ሰዎች” የሚለው ሐረግ ከጋዛ የሆኑትን ሰዎች ያመለክታል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የሆነ ሰው ለጋዛ ሰዎች ነግሯቸዋል” (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

የጋዛ ሰዎች ቦታውን ከበቡት --- ሌሊቱን ሙሉ በከተማው በር ጠበቁት

ይህ የሚያመለክተው አንዳንድ የጋዛ ሰዎች ሳምሶን ያረፈበትን ቦታ መክበባቸውንና ሌሎቹ ደግሞ እንዳያመልጥ የከተማውን በር መጠበቃቸውን ነው።

ሌሊቱን ሙሉ ፀጥ አሉ

ትርጓሜዎች ሊሆኑ የሚችሉት 1) “ሌሊቱን ሙሉ ምንም ዓይነት ድምፅ አላሰሙም” ወይም 2) “ሌሊቱን ሙሉ እርሱን ለማጥቃት ምንም ዓይነት ሙከራ አላደረጉም”።

Judges 16:3

እስከ እኩለ ሌሊት

“እስከ ሌሊቱ አጋማሽ ድረስ”

ሁለቱን መቃኖች

እነዚህ ለከተማው በር ድጋፎች ናቸው። እነዚህ መቃኖች ምናልባትም ከዛፍ ግንድ የተሰሩና በምድር ውስጥ በጥልቀት የተቀበሩ ናቸው። የከተማው በር መዝጊያዎች ከነዚህ መቃኖች ጋር የተያያዙ ነበሩ።

ቋሚ ብረቱንና ሁሉንም

ቋሚው ብረት በሮቹን ከመቃኑ ጋር ያያዙ ከባድ የብረት ቋሚዎች ሳይሆኑ አይቀሩም። የከተማይቱ በር መዝጊያዎች ምናልባትም ከከባድ እንጨት ወይም የብረት ቋሚዎች የተሠሩ ይሆናሉ።

ትከሻዎች

ክንድንና አንገትን ከሰውነት ጋር የሚያያይዘው የሰውነት ክፍል

ኬብሮን

ይህ የከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 16:4

የሶሬቅ ሸለቆ

ይህ በሳምሶን ቤት አቅራብያ የሚገኝ ሸለቆ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ተንኮል

እነርሱ ሊያደርጉት የማይፈልጉትን ነገር ሌላው ሰው እንዲያደርገው ማሳሳት ወይም ማታለል

ለማየት

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን አንድን ነገር መማር ማለት ነው። አ.ት፡ “መረዳት” ወይም “መማር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ታላቅ ብርታቱ ያለበትን

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ኃይሉ ከየት እንደሚመጣ የሚያመለክት ነው። አ.ት፡ “በጣም ጠንካራ እንዲሆን የሚያደርገው ምንድነው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በምን መንገድ ልናሸንፈው እንችላለን

“እንዴት እናሸንፈው እንደሆን”

1,100 የብር ሰቅል

“አንድ ሺህ አንድ መቶ የብር ሰቅል”። (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 16:6

በቁጥጥር ስር እንድትሆን የምትታሰረው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በቁጥጥር ስር እንድትሆን ለማሰር” ወይም “አስሮ ለመግታት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

አዲስ ጠፍሮች

አብዛኛውን ጊዜ ጠፍር የሚዘጋጀው ከእንስሳ ቆዳ፤ በተለይም ከጅማት ይሠራል። “አዲስ ጠፍር” የሚሉት ቃላት በቅርብ ከታረደ እንስሳ የመጣና ያልደረቀ መሆኑን ያመለክታል።

ያልደረቀ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እስካሁን ያልደረቁ” ወይም “ገና ያልደረቁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 16:8

ያልደረቁ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እስካሁን ያልደረቁ” ወይም “ገና ያልደረቁ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በእነርሱ ሳምሶንን አሰረችው

“ደሊላ ሳምሶንን በአዲሶቹ ጠፍሮች አሰረችው”

አሁን

ይህ ቃል ጥቅም ላይ የዋለው ዋናው የትረካ መስመር ለአፍታ መገታቱን ለማሳየት ነው። እዚህ ጋ ደራሲው ደሊላ ሳምሶንን እንዲማርኩ ስለምታስጠብቃቸው ፍልስጥኤማውያን ዳራዊ መረጃ ይናገራል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ፍልስጤማውያን ባንተ ላይ ናቸው

“ባንተ ላይ” የሚለው ሐረግ ሊይዙት ተዘጋጅተዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “ፍልስጥኤማውያኑ ሊይዙህ እዚህ ናቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

እሳት እንደነካው የሱፍ ክር ጠፍሮቹን በጣጠሳቸው

ደራሲው የሱፍ ክር ሲቃጠል እንደሚቀልጥ የሳምሶንን በቀላሉ ጠፍሮቹን መበጣጠስ እያነጻጸረ ያብራራል። አ.ት፡ “የሱፍ ክርን እንደሚያቃጥል ጠፍሮቹን በቀላሉ በጣጠሳቸው” ወይም “ከስስ የሱፍ ክር የተሠሩ ይመስል በቀላሉ ጠፍሮቹን በጣጠሳቸው”

Judges 16:10

እንደዚህ ነው ያታለልከኝና የዋሸኸኝ

ማታለልና መዋሸት ተመሳሳይ ሲሆኑ ደሊላ ምን ያህል እንደተናደደች አጽንዖት ለመስጠት ተነግረዋል። አ.ት፡ “እጅግ አታልለኸኛል!”

ልትሸነፍ የምትችለው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሰዎች ሊያሸንፉህ የሚችሉት”

ፍልስጤማውያን ባንተ ላይ ናቸው

“ባንተ ላይ” የሚለው ሐረግ ሊይዙት ተዘጋጅተዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “ፍልስጥኤማውያኑ ሊይዙህ እዚህ ናቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ተቀምጠው ይጠባበቁት ነበር

ይህ ማለት ተደብቀው ለማጥቃት ትክክለኛውን ጊዜ እየጠበቁ ነበር ማለት ነው። አ.ት፡ “ሊያጠቁት እየጠበቁ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የክር ቁራጭ እንደሆኑ ያህል

ደራሲው ሳምሶን ክርን እንደሚበጣጥስ በቀላሉ ገመዶቹን እንደበጣጠሰ በማነጻጸር ያብራራል። አ.ት፡ “የክር ቁራጭ የሆኑ ያህል በቀላሉ”

Judges 16:13

አታልለኸኛል፣ ዋሽተኸኛልም

ማታለልና መዋሸት ተመሳሳይ ሲሆኑ ደሊላ ምን ያህል እንደተናደደች አጽንዖት ለመስጠት ተነግረዋል። አ.ት፡ “እጅግ አታለኸኛል”

ልትሸነፍ የምትችለው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሰዎች ሊያሸንፉህ የሚችሉት” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

መጎንጎን

የቁሳቁሶችን ቁርጥራጭ በማሰባጠር እርስ በእርስ እንዲያያዙ ማድረግ።

የፀጉሬን ጉንጉን

ትናንሽ የፀጉር ስብስቦች

ፈትል

ቁሳቁሶችን በመሸመን የሚሰራ ልብስ

የሸማኔ እቃ

የተለያዩ የክር ዓይነቶችን ልብስ አድርጎ ለማያያዝ የሚጠቅም መሳርያ። (የማይታወቁትን መተርጎም የሚለውን ተመልከት)

ከሸማኔ ዕቃው ጋር ቸንክሪው

“ጨርቁን ከሸማኔው ዕቃ ጋር ቸንክሪው”

መቸንከር

የሆነን ነገር በቦታው ለመያዝ በመዶሻ ሚስማር መምታት

እንደ ማንኛውም ሰው እሆናለሁ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እንደ ማንኛውም ሰው ደካማ እሆናለሁ”

ፍልስጤማውያን ባንተ ላይ ናቸው

“ባንተ ላይ” የሚለው ሐረግ ሊይዙት ተዘጋጅተዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “ፍልስጥኤማውያኑ ሊይዙህ እዚህ ናቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ፈትሉና ችካሉን ነቀለው

ሳምሶን ፀጉሩን ከሸማኔው ዕቃ ላይ ሲጎትተው ከነፈትሉ ነቀለው። ይህ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ፀጉሩን ከሸማኔ ዕቃ፣ ከችካሉና ከፈትሉ ጋር ጎተተው”

ችካሉ

ፈትሉን ከሸማኔው ዕቃ ጋር የሚያያይዘው ከእንጨት የተሰራ ችንካር ወይም ችካል ነው።

Judges 16:15

ምስጢርህን ሳታክፍለኝ እንዴት “እወድሻለሁ” ትለኛለህ?

ሳምሶን በርግጥ የሚወዳት ቢሆን ኖሩ ምስጢሩን ይነግራት እንደነበር ለመናገር ደሊላ ይህንን ጥያቄ ትጠይቃለች። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “ምስጢርህን አታካፍለኝምና ‘እወድሻለሁ’ በምትልበት ጊዜ እየዋሸህ ነው” (ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ነዘነዘችው ጨቀጨቀችው

እዚህ ጋ ደራሲው ደሊላ ለማወቅ ምትፈልገውን ነገር ሳምሶን እንዲነግራት ለማሳመን ግፊት ያደረገችበት ይመስል ሳምሶንን ለማግባባት እንዴት እንደምትሞክር ይናገራል። አ.ት፡ “ልታግባባው በጣም ሞከረች … ለማግባባት መሞከሯን ቀጠለች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በቃሎቿ

“እርሱን በምትናገረው ንግግር”

ሞቱን እስኪመኝ ድረስ

ደራሲው እዚህ ጋ ሳምሶን ምን ያህል ምሬት እንደተሰማው አጽንዖት ለመስጠት ግነትን ይጠቀማል። አ.ት፡ “ፈፅሞ እንደመረረው” ወይም “እጅግ እንዳዘነ” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

Judges 16:17

ሁሉንም ነገር ነገራት

ስለ ብርታቱ ምንጭ ሁሉንም ነገር ነገራት። ይህ በግልጽ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “የብርታቱን ምንጭ ነገራት” ወይም “እውነቱን ነገራት”

ምላጭ

ከሰው ቆዳ ድረስ ተጠግቶ ፀጉር ለመቁረጥ የሚያገለግል ስለታም መቁረጫ

ለእግዚአብሔር ናዝራዊ

ይህ ማለት እንደ ናዝራዊ ለእግዚአብሔር የተሰጠ ነበር ማለት ነው። በመሳፍንት 13፡15 ያለውን ተመሳሳይ ሐረግ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ለእግዚአብሔር የተሰጠ ናዝራዊ” ወይም “እንደ ናዝራዊ ለእግዚአብሔር የተሰጠ”

ከእናቴ ማህፀን

እዚህ ጋ “ከእናቴ ማህፀን” የሚያመለክተው የተወለደበትን ጊዜ ነው። ይህ ማለት ከተወለደበት ጊዜ ጀምሮ ናዝራዊ ነበር ማለት ነው። አ.ት፡ “ሕይወቴን በሙሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ፀጉሬ ከተላጨ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው ፀጉሬን ቢላጨኝ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ተላጨ

ወደ ቆዳ አስጠግቶ ፀጉርን በምላጭ መቁረጥ

ኃይሌ ከእኔ ይሄዳል

ሳምሶን ስለ ብርታቱ ትቶት ሊሄድ እንደሚችል ሰው አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “ከእንግዲህ ወዲህ ብርቱ አልሆንም” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

Judges 16:18

ደሊላ ተመለከተች

እዚህ ጋ “ተመለከተች” የሚለው ቃል የሆነን ነገር መገንዘብ የሚል የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ደሊላ ተገነዘበች” ወይም “ደሊላ ዐወቀች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ስለ ሁሉም ነገር እውነታውን

እዚህ ጋ “ሁሉም ነገር” የሚለው ቃል ስለ ሳምሶን ጥንካሬ ሁሉንም ነገር የሚያመለክት ነው። አ.ት፡ “ብርቱ ስለሆነበት እውነታ”

እንደገና ወደ ላይ ኑ

ደሊላ ገዢዎቹን እንደገና ወደ መኖያዋ እንዲመጡ እየነገረቻቸው ነው። የእርሷ ቤት ገዢዎቹ ከሚጓዙበት ከፍ ያለ ቦታ ላይ ሳይሆን አይቀርም።

ብሩን በእጆቻቸው ይዘው

ይህ ሳምሶንን ለመያዝ ከረዳቻቸው ሊሰጧት ቃል የገቡላትን ብር ወደ እርሷ አምጥተዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “ሊሰጧት ቃል የገቡላትን ብር በመያዝ”

አስተኛችው

“እንቅልፍ እንዲወስደው አደረገችው”

በጭኗ ላይ

ይህ ማለት ጭንቅላቱን ጭኗ ላይ አድርጎ ተኝቷል ማለት ነው። ይህ በግልጽ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “ጭንቅላቱ በጭኗ ላይ ሆኖ”

ጭን

ጭን ሰው ሲቀመጥ ደልደል የሚለው የላይኛው እግር ክፍል ነው።

ሰባቱን የፀጉር ጉንጉኖቹን

ሳምሶን በራሱ ላይ ሰባት የፀጉር ጉንጉኖች ነበሩት። ጉንጉኖች ትናንሽ የፀጉር ክምችቶች ናቸው። እዚህ ጋር ሰባቱ የፀጉሩ ጉንጉኖች “የእርሱ” መባላቸው የጭንቅላቱ ንብረቶች እንደሆኑ ተደርገው ተገልጸዋል። አ.ት፡ “በራሱ ላይ የነበሩት ሰባቱ የፀጉር ጉንጉኖች” (ንብረት የሚለውን ተመልከት)

አሸነፉት

“በቁጥጥር ስር አዋሉት”

ብርታቱ ተለይቶት ነበር

እዚህ ጋ የሳምሶን ብርታት ትቶት ሊሄድ እንደሚችል ሰው ተደርጎ ተገልጿል። አ.ት፡ “ብርታቱ ሄዶ ነበር” ወይም “ከእንግዲህ ብርቱ አልሆነም” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

Judges 16:20

ዐይኖቹን አወጡት

ይህ ማለት ዐይኖቹን ከጭንቅላቱ አውጥተዉታል ማለት ነው። “ዐይኖቹን አጠፏቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ወደ ታች ወደጋዛ

“ወደ ታች” የሚለው ሐረግ እዚህ ጋ ጥቅም ላይ የዋለው ሳምሶንን ከያዙበት ከቤቱ በከፍታው ዝቅ ወዳለው ወደ ጋዛ ስለ ወሰዱት ነው።

በነሐስ የእግር ብረት አሰሩት

“ከነሐስ የእግር ብረት ጋር አሰሩት” ወይም “የነሐስ የእግር ብረት በመጠቀም አሰሩት”

የእግር ብረት

በሰንሰለት መጨረሻ ላይ ያለ የእስረኛውን እግር ወይም እጅ ወይም ሁለቱንም ለማሰር የሚጠቅም መቆለፊያ ያለው

በድንጋይ ወፍጮ ይፈጭ ነበር

“የድንጋይ ወፍጮውን በክብ ይጎትት ነበር”

የድንጋይ ወፍጮ

ይህ በጣም ትልቅ፣ ከባድና ክብ ድንጋይ ነው። ተለቅ ያለ እንስሳ የድንጋይ ወፍጮውን በክብ ዓይነት እየሳበ እህል መፍጨቱ የተለመደ ነበር። እዚህ ጋ ፍልስጥኤማውያን ሳምሶን እንዲጎትተው በማድረግ እያዋረዱት ነው።

ከተላጨ በኋላ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ፍልስጥኤማውያን ከላጩት በኋላ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 16:23

ዳጎን

ከፍልስጥኤማውያን ሐሰተኛ አማልክት ዋነኛው (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ድል ስለ ሰጠን

“ስላሸነፈልን”

በእጃችን እንዲገባ ስላደረግህ

እዚህ ጋ ደራሲው በገዢዎቹ ቁጥጥር ስር ስለሆነው ሳምሶን በእጃቸው ጥብቅ ተደርጎ እንደተያዘ አንዳች ነገር አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “በቁጥጥራችን ስር አድርጎታል” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

የሀገራችን አጥፊ

ይህ የሚያመለክተው ሳምሶንን ነው። “አጥፊ” የሚለው ቃል “አጠፋ” በሚለው ግሥ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሀገራችንን ያጠፋው ሰው”

ከእኛ ብዙዎቹን የገደለ

እዚህ ጋ “እኛ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው ፍልስጥኤማውያንን ነው። ተናጋሪዎቹ ሳሞሶን ከገደላቸው ሰዎች መካከል ራሳቸውን እየቆጠሩ አይደለም። አ.ት፡ “ከእኛ ሰዎች ብዙዎቹን የገደለ”

Judges 16:25

ሳምሶንን ጥሩት ሳምሶንን ጠሩት

ሳምሶን እስረኛ ስለነበር በቀጥታ መጠራት አይችልም ነበር፤ ነገር ግን ሰዎቹ የእስር ቤቱን ኃላፊዎች ሳምሶንን ወደ እነርሱ እንዲያመጡላቸው እየጠየቁ ነበር። አ.ት፡ “ሳምሶንን እንዲያመጡላቸው ጠየቋቸው ሳምሶንን አመጡት”

ልጁ

“ታዳጊው ልጅ” ይህ ትንሽ ልጅ አልነበረም፣ ይልቁንም ወጣት ነው።

ሕንጻው ያተደገፈበትን ምሰሶ እንድነካ ፍቀድልኝ

“ሕንጻውን ደግፈው የያዙትን ቋሚዎች እንድነካ ፍቀድልኝ”

Judges 16:27

አሁን

ይህ ቃል እዚህ ጋ ጥቅም ላይ የዋለው ደራሲው ስለ ዳራዊ መረጃ ሊናገር ከዋናው ታሪክ ለአፍታ መውጣቱን ለማመልከት ነው። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ሶስት ሺህ ወንዶችና ሴቶች

“3,000 ወንዶችና ሴቶች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

እየተመለከቱ

“እያዩ”

ሳምሶን እያዝናናቸው እያለ

ሳምሶን እነርሱን ለማዝናናት ምን እንዳደረገ ግልጽ አይደለም። ፍልስጥኤማውያን እንዲቀልዱበት፣ ሊያዋርዱት የሚችሉ ነገሮችን ያስደረጉት ይመስላል።

Judges 16:28

ወደ እግዚአብሔር ተጣራ

“ወደ እግዚአብሔር ጸለየ”

አስበኝ

ይህ ማለት እርሱንና ያለበትን ሁኔታ እንዲያስታውስ ማለት ነው። አ.ት፡ “አስታውሰኝ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ይህን አንድ ጊዜ ብቻ

“አንድ ጊዜ ብቻ”

በአንድ ጊዜ ፍልስጥኤማውያን ላይ

ይህ የአነጋገር ዘይቤ፣ ፍልስጥኤማዊያን ስላደረጉበት ነገር ፈጽሞ ለመበቀል በእነርሱ ላይ አንድ ጊዜ የኃይል ድርጊት ለመፈጸም ይፈልጋል ማለት ነው። አ.ት፡ “በፍልስጥኤማውያን ላይ በአንድ ምት” ወይም “በፍልስጥኤማውያን ላይ በአንድ ኃይለኛ ድርጊት” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሕንጻው ያረፈበት

“ሕንጻውን ባቆመው”

Judges 16:30

በብርታቱ ገፋው

ሳምሶን ክንዶቹን ሲዘረጋ የሕንጻውን ምሰሶዎች ገፍቶ ጣላቸው። አ.ት፡ “ምሰሶዎቹን ለመጣል ብርታቱን ተጠቀመ” ወይም “ምሰሶዎቹን ለመግፋት ኃይሉን ተጠቀመ”

የሞቱት

ይህ የሞቱትን ሰዎች ያመለክታል። “የሞቱት ሰዎች”

ይበዙ ነበር

“በቁጥር ብዙ ነበሩ”

የአባቱ ቤት ሁሉ

እዚህ ጋ “ቤት” የሚለው ቃል የሚያመለክተው የእርሱን ቤተሰብ ነው። አ.ት፡ “የአባቱ ቤተሰቦች በሙሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ወረዱ

“ወረዱ” የሚለው ቃል እዚህ ጋ ጥቅም ላይ የዋለው የሳምሶን ቤተሰብ የተጓዘበት ቦታ ከጋዛ በከፍታ የሚበልጥ ስለነበረ ነው።

ጾርዓ ኤሽታኦል

የእነዚህን ቦታዎች ስም በመሳፍንት 13፡2 እና በመሳፍንት 13፡25 እንዴት እንደተረጎምካቸው ተመልከት።

በአባቱ በማኑሔ የመቃብር ስፍራ

“አባቱ ማኑሔህ በተቀበረበት ስፍራ”

ማኑሔ

የዚህን ሰውዬ ስም በመሳፍንት 13፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሳምሶን ለሃያ ዓመታት በእስራኤል ላይ ፈርዶ ነበር

ይህ ዐረፍተ ነገር ራሱ በመሳፍንት 15፡20 ላይ አለ። እዚህ ጋ የተደገመው ለምን ያህል ጊዜ በእስራኤል ላይ እንደፈረደ አንባቢዎችን ለማስታወስ ነው። አ.ት፡ “ሳምሶን ከመሞቱ በፊት በእስራኤል ላይ ለሃያ ዓመታት ፈርዷል”

ሃያ ዓመታት

“20 አመታት” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)


Chapter 17

1 በኮረብታማውም በኤፍሬም አገር አንድ ሰው ነበር፣ ስሙም ሚካ ይባላል፡፡ 2 ለእናቱም እንዲህ አላት፣ “ከአንቺ ዘንድ ተወስዶ የነበረው 1, 100 ብር፣ የእርግማን ንግግር የተናገርሽበትና እኔም የሰማሁት እነሆ እዚህ አለ! ብሩ በእኔ ዘንድ አለ፡፡ እኔ ሰርቄዋለሁ!” እናቱም እንዲህ አለች፣ “ልጄ ሆይ፣ እግዚአብሔር ይባርክህ!” 3 እርሱም 1, 100 ብር ለእናቱ መለሰላት፣ እናቱም እንዲህ አለችው፣ “ስለ ልጄ የተቀረጸ የእንጨት ምስልና ቀልጦ የተሠራ ምስል ለማድረግ ይህን ብር ለእግዚአብሔር ለይቼዋለሁ፡፡ ስለዚህ አሁን፣ ለአንተ መልሼዋለሁ፡፡” 4 ለእናቱም ገንዘቡን በመለሰላት ጊዜ፣ እናቱ ሁለቱን መቶ ብር ወሰደችና የተቀረጸ የእንጨት ምስልና ቀልጦ የተሠራ ምስል አድርጎ ለሰራው ለብረት ሰራተኛ ሰጠችው፡፡ ያም በሚካ ቤት ተቀመጠ፡፡ 5 ሚካ የተባለውም ሰው የጣዖታት አምልኮ ቤት ነበረውና አንድ ኤፉድና ተራፊም ሰራ፣ ከልጆቹም አንዱ ካህን ሆኖ እንዲያገለግለው አደረገ፡፡ 6 በዚያን ዘመን በእስራኤል ዘንድ ንጉሥ አልነበረም፣ ሰውም ሁሉ በዓይኖቹ ፊት ትክክል መስሎ የታየውን ያደርግ ነበር፡፡ 7 አሁን በቤተ ልሔም ይሁዳ ከይሁዳ ወገን የሆነ አንድ ሌዋዊ ወጣት ሰው ነበረ፡፡ እርሱም ተግባሩን ለመፈጸም በዚያም ይቀመጥ ነበር፡፡ 8 ይህ ሰው የሚቀመጥበትን ስፍራ ለመፈለግ ቤተ ልሔም ይሁዳን ለቅቆ ሄደ፡፡ ሲጓዝም ወደ ኮረብታማው የኤፍሬም አገር ወደ ሚካ ቤት መጣ፡፡ 9 ሚካም ለእርሱ እንዲህ አለው፣ “ከወዴት መጣህ?” እርሱም እንዲህ አለው፣ “እኔ ከቤተ ልሔም ይሁዳ የመጣሁ ሌዋዊ ነኝ፣ የምኖርበትን ስፍራ ለማግኘት እየተጓዝሁ ነው፡፡” 10 ሚካም እንዲህ አለው፣ “ከእኔ ጋር ተቀመጥ፣ ለእኔም አማካሪና ካህን ሁነኝ፡፡ እኔም በየዓመቱ አሥር ብር፣ እንደዚሁም ልብሶችንና ምግብህን እሰጥሃለሁ፡፡” ስለዚህ ሌዋዊው ወደ ቤቱ ገባ፡፡ 11 ሌዋዊውም ከሰውዮው ጋር ለመቀመጥ ፈቃደኛ ሆነ፣ ወጣቱም ሰው ለሚካ ከልጆቹ እንደ አንዱ ሆነለት፡፡ 12 ሚካም ሌዋዊውን ለተቀደሰ ሃላፊነት ቀደሰው፣ ወጣቱም ሰው ካህኑ ሆነለት፣ በሚካም ቤት ነበረ፡፡ 13 ከዚያም ሚካ እንዲህ አለ፣ “አሁን እግዚአብሔር ለእኔ መልካም እንደሚሰራልኝ አውቄአለሁ፣ ምክንያቱም ይህ ሌዋዊ ካህን ሆኖልኛል፡፡”



Judges 17:1

አንድ ሰው ነበር

ይህ በታሪክ ፍሰቱ ላይ አዲስን ሰው የማስተዋወቂያ መንገድ ነው። (አዲስና ነባር ተሳታፊዎችን ማስተዋወቂያ የሚለውን ተመልከት)

ሚካ

ይህ የአንድ ሰው ስም ነው። ይህ የሚክያስን መጽሐፍ የጻፈው ሰው አይደለም። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

1,100 ሰቅል

“አንድ ሺህ አንድ መቶ ሰቅል” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ከአንቺ የተወሰደው

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንድ ሰው የሰረቀብሽ” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ሰርቄዋለሁ

“እኔ ነኝ የወሰድኩት”

Judges 17:3

1,100 ሰቅል

“አንድ ሺህ አንድ መቶ ሰቅል” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ለየ

ይህ ማለት አንድን ነገር ለተለየ አላማ መስጠት ማለት ነው። አ.ት፡ “ተሰጠ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የቀለጠ ብረት

የተለየ ቅርጽ ለማውጣት በቅርጽ ማውጫ ውስጥ ቀልጦ የሚጨመር ብረት

እመልስልሃለሁ

“ላንተ መልሼ እሰጥሃለሁ”

ሁለት መቶ ሰቅል ብር

“200 ሰቅል ብር” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

እነርሱ በሚካ ቤት ተቀምጠው ነበር

“እነርሱ” የሚለው ቃል የብረት ቅርጾቹን ያመለክታል። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ሚካ በቤቱ አስቀምጧቸው ነበር” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 17:5

የጣዖታት ቤት

ይህ በግልጽ ጣዖታት የሚመለኩበትን ቤት ያመለክታል። ይህ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ጣዖታትን የማምለኪያ ቤት”

ሁሉም በዐይኖቹ መልካም መስሎ የታየውን ያደርግ ነበር

ዐይን ዕይታን ይወክላል፤ ማየትም አሳብን ወይም ውሳኔን ይወክላል። አ.ት፡ “እያንዳንዱ ሰው ልክ ነው ብሎ የወሰነውን ያደርግ ነበር” ወይም “እያንዳንዱ ሰው ልክ ነው ብሎ የፈረደውን ያደርግ ነበር” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 17:7

የቤተልሔም

“ከቤተልሔም”

ከይሁዳ ነገድ የሆነ

ይህ ማለት በይሁዳ ቤተሰቦች ይኸውም በይሁዳ ነገድ መካከል ይኖር ነበር ማለት ነው። አ.ት፡ “በይሁዳ ነገድ መካከል ይኖር የነበረ”

ኃላፊነቱን ለመወጣት በዚያ ይኖር ነበር

“በዚያ ይኖርና ይሠራ ነበር”

መኖሪያ እየፈለገ

“ሌላ የመኖርያ ቦታ ለመፈለግ”

የምኖርበትን

የሚኖርበትንና የሚሠራበትን ቦታ እየፈለገ እንደሆነ ያመለክታል። አ.ት፡ “የምኖርበትና የምሠራበትን ስፍራ”

Judges 17:10

አባትና ካህን

“አባት” የሚለው ቃል እዚህ ጋ አማካሪ ለማለት ጥቅም ላይ ውሏል እንጂ እውነተኛ አባትነትን አያመለክትም። አ.ት፡ “አማካሪና ካህን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በዓመት አሥር ሰቅል ብር እሰጥሃለሁ

“በየዓመቱ አሥር ጥሬ ብር እሰጥሃለሁ”

ቅያሪ ልብስ

“የልብሶች ስብስብ”

ስለዚህ ሌዋዊው ወደ እርሱ ቤት ገባ

ሌዋዊው የሚካን አሳብ መቀበሉንና ወደ ሚካ ቤት መግባቱን ያመለክታል። አ.ት፡ “ስለዚህ ሌዋዊው ግብዣውን ተቀብሎ ወደ ቤቱ ገባ”

ወጣቱ ለሚካ ከወንዶች ልጆቹ እንደ አንዱ ሆነለት

በሌዋዊውና በሚካ መካከል ያለው ግንኙነት እንደ አባትና ልጅ የጠበቀ ሆነ። አ.ት፡ “ወጣቱ ከሚካ ጋር በጣም ከመቀራረቡ የተነሣ ከወንዶች ልጆቹ እንደ አንዱ ሆነ”

Judges 17:12

ሚካ ሌዋዊውን ለየው

እዚህ ጋ “ለየው” ማለት ሚካ “ቀደሰው” ወይም “ሾመው” ማለት ነው። አ.ት፡ “ሚካ ሌዋዊውን ቀደሰው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በሚካ ቤት ነበረ

እዚህ ጋ በሚካ ቤት መኖሩ በቤቱ “እንደሆነ” ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “በሚካ ቤት ኖረ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 18

1 በዚያን ዘመን በእስራኤል ውስጥ ንጉሥ አልነበረም፡፡ የዳን ነገድ ተወላጆች የሚቀመጡበትን ርስት ይፈልጉ ነበር፣ እስከዚያ ቀን ድረስ በእስራኤል ነገዶች መካከል ርስት አልተቀበሉም ነበርና፡፡ 2 የዳን ሰዎች ከአጠቃላይ ወገናቸው በሙሉ ከጾርዓ ጀምሮ እስከ ኤሽታኦል ድረስ በጦርነት ልምድ ያላቸውን አምስት ሰዎች በእግራቸው ሄደው ምድሪቱን እንዲሰልሉና እንዲያዩ ላኩ፡፡ ለእነርሱም እንዲህ አሉአቸው፣ “ሂዱና ምድሪቱን ሰልሉ፡፡” እነርሱም ወደ ኮረብታማው ወደ ኤፍሬም አገር ወደ ሚካ ቤት መጡና ሌሊቱን በዚያ አሳለፉ፡፡ 3 በሚካ ቤት አጠገብ በነበሩ ጊዜ፣ የአንድ ወጣት ሌዋዊ ንግግር አወቁ፡፡ ስለዚህ አስቆሙትና እንዲህ ብለው ጠየቁት፣ “ወደዚህ ማን አመጣህ? በዚህ ስፍራ ምን ታደርጋለህ? ለምን ወደዚህ መጣህ?” 4 እርሱም እንዲህ አላቸው፣ “ሚካ ለእኔ ያደረገው ነገር ይህ ነው፡- የእርሱ ካህን እንድሆን ቀጠረኝ፡፡” 5 እነርሱም እንዲህ አሉት፣ “የምንሄድበት መንገድ መቃናቱን ወይም አለመቃናቱን እናውቅ ዘንድ፣ እባክህ፣ የእግዚአብሔርን ምክር ጠይቅልን፡፡” 6 ካህኑም ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ “በሰላም ሂዱ፡፡ ልትሄዱ በሚገባችሁ መንገድ እግዚአብሔር ይመራችኋል፡፡” 7 የዚያን ጊዜ አምስቱ ሰዎች ሄዱና ወደ ላይሽ መጡ፣ ሲዶናውያን በጸጥታ ያለስጋት ይኖሩ እንደነበረ ሁሉ፣ በዚያም ተዘልለው ይኖሩ የነበሩትን ሕዝብ አዩ፡፡ በምድሪቱም በየትኛውም መልኩ የገዛቸው፣ ወይም ያስቸገራቸው አልነበረም፡፡ ከሲዶናውያን በጣም ርቀው ይኖሩ ነበር፣ ከማንኛውም ሕዝብ ጋር ምንም ግንኙነት አልነበራቸውም፡፡ 8 በጾርዓና በኤሽታኦል ውስጥ ወደነበሩት ወንድሞቻቸው ተመለሱ፡፡ ዘመዶቻቸውም እንዲህ ብለው ጠየቁአቸው፣ “ምን ወሬ ይዛችኋል?” 9 እነርሱም እንዲህ አሉ፣ “ኑ! እንውጋቸው! ምድሪቱን አይተናታል፣ በጣም ጥሩ ናት፡፡ እናንተ ዝም ትላላችሁን? ምድሪቱን ከመውጋትና ከመውረስ አትዘግዩ፡፡ 10 በሄዳችሁ ጊዜ፣ ያለ ስጋት እንደሚኖሩ ወደሚያስቡ ሕዝብ ትደርሳላችሁ፣ ምድሪቱም ሰፊ ናት! እግዚአብሔርም ለእናንተ ሰጥቶአችኋል፣ በምድር ካለው ነገር ሁሉ አንዳች የማይጎድልባት ስፍራ ናት፡፡ 11 ከዳን ወገን የሆኑና የጦር መሳርያ የታጠቁ ስድስት መቶ ሰዎች ከጾርዓና ከኤሽታኦል ተነሥተው ሄዱ፡፡ 12 እነርሱም ሄዱና በይሁዳ ባለችው በቂርያትይዓሪም ሰፈሩ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ የዚያ ስፍራ ስም የዳን ሰፈር ብለው የሚጠሩት ለዚህ ነው፤ እርሱም ከቂርያትይዓሪም በምዕራብ በኩል ነው፡፡ 13 እነርሱም ከዚያ ተነስተው ወደ ኮረብታማው የኤፍሬም አገር አልፈው ሄዱ፣ ወደ ሚካም ቤት መጡ፡፡ 14 ከዚያም የላይሽን አገር ሊሰልሉ ሄደው የነበሩት አምስቱ ሰዎች ለዘመዶቻቸው እንዲህ አሉአቸው፣ “በእነዚህ ቤቶች ውስጥ ኤፉድና ተራፊም፣ የተቀረጸ ምስልና ቀልጦ የተሠራ ምስል እንዳሉ ታውቃላችሁን? ምን እንደምታደርጉ አሁን ወስኑ፡፡” 15 ስለዚህ ከዚያ ዘወር አሉና ወጣቱ ሌዋዊ ይኖርበት ወደነበረው ወደ ሚካ ቤት መጡ፤ ሰላምታም አቀረቡለት፡፡ 16 በዚያን ጊዜ የጦር መሳርያ የታጠቁት ስድስት መቶ ዳናውያን በበሩ መግቢያ ቆሙ፡፡ 17 ካህኑ የጦር መሳርያ ከታጠቁት ከስድስት መቶ ሰዎች ጋር በበሩ አካባቢ ቆሞ በነበረበት ጊዜ፣ ምድሪቱንም ሊሰልሉ ሄደው የነበሩት አምስቱ ሰዎች ወደዚያ ሄዱና የተቀረጸውን ምስል፣ ኤፉዱን፣ ተራፊሙንና ቀልጦ የተሠራውን ምስል ወሰዱ፡፡ 18 እነዚህ ወደ ሚካ ቤት ገብተው የተቀረጸውን ምስል፣ ኤፉዱን፣ ተራፊሙንና ቀልጦ የተሠራውን ምስል በወሰዱ ጊዜ፣ ካህኑ ለእነርሱ እንዲህ አላቸው፣ “ምን ታደርጋላችሁ?” 19 እነርሱም እንዲህ አሉት፣ “ዝም በል! እጅህን በአፍህ ላይ ጫንና ከእኛ ጋር ና፣ ለእኛም አባትና ካህን ሁንልን፡፡ ለአንተስ ለአንድ ሰው ቤት ካህን መሆን ወይስ በእስራኤል ውስጥ ላለው ነገድና ወገን ሁሉ ካህን መሆን ይሻልሃል?” 20 የካህኑም ልብ ደስ አለው፡፡ ኤፉዱን፣ ተራፊሙንና የተቀረጸውንም ምስል ወሰደና ከሕዝቡ ጋር ሄደ፡፡ 21 ስለዚህ እነርሱ ዞሩና ሄዱ፡፡ ሕፃናቶችን፣ ከብቶችንና ንብረታቸውን በፊታቸው አስቀደሙ፡፡ 22 ከሚካም ቤት ጥቂት በራቁ ጊዜ፣ በሚካ ቤት አጠገብ በነበሩት ቤቶች ውስጥ የነበሩ ሰዎች ተጠራርተው ተሰበሰቡ፣ የዳን ሰዎችንም ተከትለው ደረሱባቸው፡፡ 23 ወደ ዳንም ሰዎች ጮኹ፣ ዘወር ብለው ለሚካም እንዲህ አሉት፣ “ተሰብስባችሁ በአንድ ላይ የመጣችሁት ለምንድን ነው?” 24 እርሱም፣ “የሠራኋቸውን አማልክቴን ሰረቃችሁ፣ ካህኔንም ይዛችሁ ሄዳችሁ፡፡ ሌላ ምን የቀረኝ ነገር አለ? ‘ያስጨነቀህ ምንድን ነው?’ ብላችሁ እንዴት ልትጠይቁኝ ትችላላችሁ፡፡” 25 የዳን ሰዎችም እንዲህ አሉት፣ “ምንም ዓይነት ንግግር ስትናገር እንድንሰማ አታድርገን፣ አለዚያ አንዳንድ የተቈጡ ሰዎች ይጎዱሃል፣ አንተና ቤተሰቦችህም ትሞታላችሁ፡፡” 26 የዚያን ጊዜ የዳን ሰዎች መንገዳቸውን ሄዱ፡፡ ሚካ ከእርሱ ይልቅ እነርሱ እጅግ በጣም የበረቱ እንደሆኑ ባየ ጊዜ፣ ተመልሶ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ 27 የዳን ሰዎችም ሚካ የሠራውን ጣዖትና ካህኑን ወሰዱና ወደ ላይሽ መጡ፣ በሰላምና ያለ ስጋት ተዘልሎም ወደ ተቀመጠው ሕዝብ መጥተው በሰይፍ ስለት ገደሉአቸው፣ ከተማይቱንም በእሳት አቃጠሉአት፡፡ 28 እነርሱን የሚያድን አንድም ሰው አልነበረም ምክንያቱም ከተማይቱ ከሲዶና በጣም ራቅ ያለች ነበረች፣ እነርሱም ከሌሎች ሰዎች ጋር ምንም ግንኙነት አልነበራቸውም፡፡ እርስዋም በቤትሮዖብ አጠገብ ባለው ሸለቆ ውስጥ ነበረች፡፡ የዳን ሰዎችም ከተማይቱን እንደገና ሠሩና ተቀመጡባት፡፡ 29 ከተማይቱንም ከእስራኤል ወንዶች ልጆች አንዱ በሆነው በአባታቸው በዳን ስም ዳን ብለው ጠሩአት፡፡ ነገር ግን አስቀድሞ የከተማይቱ ስም ላይሽ ነበረ፡፡ 30 የዳን ሰዎችም ለራሳቸው የተቀረጸ ምስል አቆሙ፣ የሙሴ ልጅ የጌርሳም ልጅ ዮናታን፣ እርሱና ወንዶች ልጆቹ ምድሪቱ እስከምትያዝበት ቀን ድረስ ለዳን ሰዎች ካህናት ነበሩ፡፡ 31 ስለዚህ የእግዚአብሔር ቤት በሴሎ በነበረበት ጊዜ ሁሉ፣ ሚካ የሰራውን የተቀረጸ ምስል አመለኩ፡፡



Judges 18:1

በእነዚያ ቀናት

ይህ ሐረግ በታሪኩ ፍሰት ላይ ሌላ አዲስ የሁነት ጅማሬን ያስተዋውቃል። (አዲስ ሁነትን ማስተዋወቅ የሚለውን ተመልከት)

በእነዚያ ቀናት… ከእስራኤል ነገዶች መካከል

ይህ ስለ እስራኤልና ስለዳን ነገድ ሕዝቦች ዳራዊ መረጃ ነው። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ምንም ርስት አልተቀበለም

ይህ በግልጽ የሚኖሩበትን መሬት እንዳልወረሱ ያመለክታል። አ.ት፡ “የመሬት ርስት አልተቀበልንም”

ከነገዳቸው በሙሉ

“በሙሉ” የሚለው ቃል በነገዱ ያሉትን ሰዎች ሁሉ ያመለክታል። አ.ት፡ “በየነገዱ መካከል ካሉት ሰዎች ሁሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ልምድ ያላቸው ጦረኞች

“ልምድ ያላቸው ተዋጊዎች”

ጾርአ

የዚህን ከተማ ስም በመስፍንት 13፡2 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ኤሽታኦል

የዚህን ከተማ ስም በመሳፍንት 13፡25 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ምድሪቱን በእግር ተጉዘው እንዲሰልሉ

“በእግር” የሚለው ሐረግ መራመድ ማለት ነው። አ.ት፡ “በእርሱ ላይ በመራመድ መሰለል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ሚካ

የዚህን ሰው ስም በመሳፍንት 17፡1 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት

Judges 18:3

የወጣቱን ሌዋዊ ንግግር ለይተው ዐወቁ

ሰውየውን በሚናገርበት ድምፁ ለይተው ዐወቁት። እዚህ ጋ “ንግግር” የሚጠቁመው “ድምፁን” ነው። አ.ት፡ “ወጣቱ ሌዋዊ ሲናገር ሰሙትና ድምፁን ዐወቁ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 18:7

ላይሽ

ይህ የከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ድል ያደረገ ማንም አልነበረም

“ድል አድርገዋቸው በምድራቸው የተቀመጡ ጠላቶች አልነበሩም”

ከማንም ጋር ምንም ግንኙነት አልነበራቸውም

“በውጪ ከሚኖሩ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት አልነበራቸውም”፤ ይህ ማለት ከሌሎች ከተሞች ርቀውና ከሌሎች ሰዎች ተገልለው ይኖሩ ነበር ማለት ነው።

ጾርአ

የዚህችን ከተማ ስም በመሳፍንት 13፡2 ላይ እንደተረጎምከው አድርገህ ተርጉም።

ኤሽታኦል

የዚህችን ከተማ ስም በመሳፍንት 13፡25 ላይ እንደተረጎምከው አድርገህ ተርጉም።

Judges 18:9

ምንም እየሠራህ አይደለም?

ይህ ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የተጠየቀው በአሽሙር ሲሆን ትርጉሙም ተቃራኒውን ማድረግ ነበረባቸው የሚል ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “አሁን የሆነ ነገር ማድረግ አለባችሁ” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ እና ድርብ አሉታ የሚለውን ተመልከት)

ለማጥቃት የዘገያችሁ አትሁኑ

እነዚህ “አትሁኑ” እና “አትዘግዩ” የሚሉት አሉታዊ ቃላቶች በአንድ ላይ በቶሎ እንዲያጠቁ አዎንታዊ አሳብ ላይ አጽንዖት የሰጣሉ። “ፍጠኑ! አጥቁ” (ድርብ አሉታ የሚለውን ተመልከት)

ምድሪቱ ሰፊ ናት

“ምድሪቱ ታላቅ ናት” ይህ የምድሩን መጠን ይገልጻል።

ምድሪቱ ምንም ነገር ያልጎደላት

ሰዎቹ ለመኖር በጣም ተመራጭ ቦታ እንደሆነ አጽንዖት ለመስጠት ግነትን ተጠቅመዋል። አ.ት፡ “በዚያ የሚያስፈልገን ነገር ሁሉ ይኖረናል” (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

ምንም ነገር ያልጎደለው

ሁለቱ አሉታዊ ቃላት በአንድነት አዎንታዊ አሳብ ላይ አጽንዖት ይሰጣሉ። አ.ት፡ “ሁሉም ነገር ያለው” (ድርብ አሉታ የሚለውን ተመልከት)

Judges 18:11

ስድስት መቶ ሰዎች

“600 ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ቂርያትይዓሪም

ይህ የከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ማኽነህ ዳን

የዚህን ስፍራ ስም በመሳፍንት 13፡25 ላይ እንደተረጎምከው አድርገህ ተርጉመው።

እስከዚህ ቀን ድረስ

ይህ ማለት የሆነ ነገር እስካሁን እንደዚያው አለ ማለት ነው። “የአሁንን ” ጊዜ ያመለክታል። አ.ት፡ “እስካሁን ስሙ እንደዚያው ነው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 18:13

ላይሽ

የዚህን ከተማ ስም በመሳፍንት 18፡7 ላይ እንደተረጎምከው አድርገህ ተርጉመው።

በእነዚህ ቤቶች ውስጥ ኤፉዶች አሉ፣ … የብረት ምስል? እናደርጋለን ወስኑ

አምስቱ ሰዎች ይህንን ጥያቄ የጠየቁት ሰዎቹ ጣዖታቱን እንዲሰርቁ አሳብ ለመስጠትና ለማደፋፈር ነው። ይህ እንደ መግለጫ ሊጻፍ ይችላል፤ አመልካች የመረጃ ሐረግም በቅንፍ ውስጥ ሊሰጥ ይቻላል። አ.ት፡ “እነዚህ ቤቶች የብረት ምስል የሆነውን ኤፉድ ይዘዋል (ሰዎቹ እንዚህን ነገሮች እንዲሰርቁ አሳብ እየሰጡ ነበር።) እናደርጋለን … ወስኑ” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ እና የሚለውን ተመልከት)

በእነዚህ ቤቶች ውስጥ አሉ

“ከእነዚህ ቤቶች በአንዱ ውስጥ አለ” ወይም “በእነዚህ ቤቶች መካከል አለ”

Judges 18:15

ወደዚያ ገቡ

“ገቡ”

ሰላምታ ሰጡት

“እርሱን” የሚለው ቃል ሌዋዊውን ያመለክታል።

ስድስት መቶ የዳን ሰዎች

“600 የዳን ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 18:17

ስድስት መቶ ሰዎች

“600 ወንዶች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 18:19

ለአንድ ሰው ቤት ካህን መሆን ይሻልሃል በእስራኤል ላለ አንድ ነገድ?

ይህንን ጥያቄ መልስ በማይሻ መልኩ የሚጠይቁት የነገሩን እውነትነት ለማመልከት ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “ለአንድ ሰው ካህን ከመሆን ይልቅ በእስራኤል ላለ ነገድ እና ጎሳ ካህን መሆን ይሻልሃል” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

የካህኑ ልብ ተደሰተ

እዚህ ጋ ካህኑ በተሰማው ስሜት ላይ አጽንዖት ለመስጠት ”ልቡ” ተብሏል። አ.ት፡ “ካህኑ ተደስቶ ነበር”

Judges 18:21

ትንንሾቹን ልጆች ከፊት ለፊታቸው አደረጓቸው

በዚህ መልኩ የሚጓዙት ልጆቹን ለመጠበቅ ነው። ሚካና ሰዎቹ ቢያጠቋቸው መጀመሪያ የሚያገኙት ጦረኞቹን እንጂ ልጆቹን አይሆንም። አ.ት፡ “ትንንሾቹን ልጆች ለመጠበቅ ከፊት ለፊታቸው አደረጓቸው”

በጥሩ ርቀት

“ጥቂት ርቀት”፣ ይህ ለመለካት የሚበቃውን ርዝመት አጭር ርቀት ይለዋል። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በሚካ ቤት አቅራብያ ባሉት ቤቶች ውስጥ የነበሩ ሰዎች አንድ ላይ ተጠርተው ነበር

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በቤቱ አቅራቢያ ባሉ ቤቶች ውስጥ የነበሩትን ሰዎች አንድ ላይ ጠራቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

በዳን ሰዎች ላይ ደረሱባቸው

ይህ ከኋላ ተከትለዋቸው እንደሮጡ ያመለክታል። ይህ በግልጽ ሊነገር ይችላል፝። አ.ት፡ “ከዳን ሰዎች ኋላ በመሮጥ ደረሱባቸው”

ወደ ኋላቸው ተመለሱ

“የዳን ሰዎች የሆኑት ወደ ኋላቸው ዞሩ”

ተጠራርታችሁ የተሰባሰባችሁት ለምንድነው?

ይህ የወቀሳ ጥያቄ ነው። እንደ መግለጫ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እኛን ለማሳደድ ሰዎችህን ጠርተህ መሰብሰብ አልነበረብህም”። (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

አንድ ላይ ተጠርተው ነበር

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “እነዚህን ሰዎች አንድ ላይ ጠሯቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 18:24

የሰራኋቸውን አማልክቶቼን

ሚካ አማልክቶቹን አልሠራቸውም፤ የሠራቸው ባለ ሙያ የሆነ ሰው ነው። አ.ት፡ “ለራሴ ያሠራኋቸውን አማልክት” ወይም “ባለ ሙያ የሠራልኝን አማልክት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሌላ ምን ቀረኝ?

ሚካ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው ለእርሱ አስፈላጊ የሆኑት ነገርች አሁን እንደሌሉት አጽንዖት ለመስጠት ነው። አ.ት፡ “ምንም የቀረኝ ነገር የለም” ወይም “ለእኔ አስፈላጊ የሆነውን ነገር በሙሉ ወስዳችሁብኛል” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

“ምን ሆንክ?” ብላችሁ እንዴት ትጠይቁኛላችሁ

ሚካ ይህንን ጥያቄ የሚጠይቀው የዳን ሰዎች የሆኑት በእርግጥ ምን እንዳሳሰበው እንደሚያውቁ አጽንዖት ለመስጠት ነው። አ.ት፡ “እጅግ እንዳዘንኩ ታውቃላችሁ!” ወይም “በእኔ ላይ ባደረጋችሁት ነገር ምን ያህል እንደተቸገርኩ ታውቃላችሁ!” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

ምንም አይነት ነገር ስትናገር እንዳንሰማህ

“ስትናገር እንዳንሰማህ” የሚለው ሐረግ የዳን ሰዎች ሚካ ስለሆነው ነገር የሚያወራውን መስማታቸውን ያመለክታል፤ ነገር ግን ሚካ ስለተፈጠረው ነገር ማውራቱን ከሌሎች ሰዎች መስማታቸውንም ይጨምራል። አ.ት፡ “ምን እንደተናገርክ ማወቅ እንፈልጋለን” ወይም “ስለዚህ ጉዳይ የፈለግኸውን ተናገር” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ምንም አይነት ነገር ስትናገር እንዳንሰማህ

“ምንም ዓይነት ነገር” የሚለው ሐረግ የዳን ሰዎች ወደ ሚካ ቤት መጥተው ጣዖቶቹን መስረቃቸውን የሚጠቁም የትኛውንም መረጃ ያመለክታል። ይህ በግልጽ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “ስለዚህ ጉዳይ ምንም ነገር ስትናገር እንዳንሰማህ” ወይም “ስለሆነው ነገር እንዳች ስትናገር እንዳንሰማህ”

አንተና ቤተሰቦችህ ትገደላላችሁ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አንተንና ቤተሰብህን እንገላለን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

መንገዳቸውን ሄዱ

ይህ ጉዟቸውን ቀጠሉ ማለት ነው። አ.ት፡ “ጉዟቸውን ቀጠሉ” ወይም “መጓዛቸውን ቀጠሉ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ለእርሱ እጅግ የበረቱ ነበሩ

ይህ የሚያመለክተው ሚካና ሰዎቹ እንዳይዋጓቸው የዳን ሰዎች እጅግ ብርቱ መሆናቸውን ነው። አ.ት፡ “እርሱና ከእርሱ ያሉት ሰዎች እንዳይዋጓቸው እጅግ ብርቱዎች ነበሩ”

Judges 18:27

ሚካ ሠርቷቸው የነበሩት

ሚካ አማልክቶቹን አልሠራቸውም፤ ይልቁን የሠራለት ባለ ሙያ ነበር። ደግሞም ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ለሚካ የተሠሩለት ነገሮች” ወይም “የሚካ ነገሮች” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ላይሽ

ይህንን በመሳፍንት 18፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

በሰይፍ ስለት

“በሰይፎቻቸው”። እዚህ ጋ “ሰይፉ” ወታደሮቹ በጦርነት የተጠቀሙባቸውን ሰይፍና ሌሎች የጦር መሳሪያዎች ይወክላል።

ከማንም ጋር ምንም ግንኙነት አልነበራቸውም ነበር

“በውጪ ከሚኖሩ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት አልነበራቸውም”፤ ይህ ማለት ከሌሎች ከተሞች ርቀውና ከሌሎች ሰዎች ተገልለው ይኖሩ ነበር ማለት ነው። ይህንን ሐረግ በመሳፍንት 18፡7 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ቤትሮዓብ

ይህ የከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 18:30

X

ይህ ሚካን በካህንነት ያገለግለው የነበረው የወጣቱ ሌዋዊ ስም ነው። ይህ ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የወጣት ሌዋዊው ስም የሙሴ ልጅ የጌርሳም ልጅ ዮናታን ነበር” ( እና ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ምድሪቱ እስከተያዘችበት ቀን ድረስ

ይህ የዳን ሰዎች በጠላቶቻቸው የሚያዙበትን የወደፊት ጊዜ የሚያመለክት ነው። እዚህ ጋ የምድሪቱ መያዝ በጠላት እንደተማረከ እስረኛ ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ጠላቶቻቸው ምድራቸውን እስከያዙበት ቀን ድረስ” ወይም “ጠላቶቻቸው ማርከው እስከወሰዷቸው ቀን ድረስ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የሠራቸው

ሚካ አማልክቶቹን አልሠራቸውም፤ ይልቁንም ባለ ሙያ ነበር የሠራለት። አ.ት፡ “ተሠርተዉለት የነበሩት” ወይም “የእርሱ ባለ ሙያ የሠራለት” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Chapter 19

1 በዚያም ዘመን፣ በእስራኤል ውስጥ ንጉሥ ባልነበረበት ጊዜ፣ በኮረብታማው የኤፍሬም አገር እጅግ በጣም ሩቅ በሆነ አካባቢ ለአጭር ጊዜ የኖረ አንድ ሌዋዊ ሰው ነበረ፡፡ እርሱም አንዲትን ሴት ቁባት አድርጎ ወሰዳት፡፡ 2 ነገር ግን ቁባቱ ለእርሱ ታማኝ አልነበረችም፤ እርሱን ተወችውና ተመልሳ ወደ አባትዋ ቤት ወደ ቤተ ልሔም ይሁዳ ሄደች፡፡ እርስዋም በዚያ አራት ወር ቆየች፡፡ 3 የዚያን ጊዜ ባልዋ ተነሣና ተመልሳ ወደ እርሱ እንድትመጣ ለማባበል ተከትሏት ሄደ፡፡ የእርሱ አገልጋይና ሁለት አህዮች ከእርሱ ጋር ነበሩ፡፡ እርስዋም ወደ አባትዋ ቤት አስገባችው፡፡የልጅቱ አባት ባየው ጊዜ ደስ አለው፡፡ 4 የልጂቱ አባት፣ አማቱም በቤቱ ለሦስት ቀን እንዲቆይ ለመነው፡፡ እነርሱም በሉ፣ ጠጡ፣ ሌሊቱንም በዚያ አሳለፉ፡፡ 5 በአራተኛው ቀን ማልደው ተነሡ፣ እርሱም ለመሄድ ተዘጋጀ፣ ነገር ግን የልጂቱ አባት አማቹን እንዲህ አለው፣ “እንድትበረታ እንጀራ ብላ፣ ከዚያ መሄድ ትችላለህ፡፡” 6 ስለዚህ ሁለቱም በአንድ ላይ ለመብላትና ለመጠጣት ተቀመጡ፡፡ ከዚያም የልጂቱ አባት እንዲህ አለ፣ “እባክህ ሌሊቱን ደግሞ እዚህ ለማሳለፍ ፈቃደኛ ሁን፣ መልካም ጊዜም ይሁንልህ፡፡” 7 ሌዋዊው ለመሄድ በማለዳ በተነሳ ጊዜ፣ የወጣቷ ሴት አባት እንዲቆይ ለመነው፣ ከዚህ የተነሳ እቅዱን ለወጠና ሌሊቱን በዚያ አሳለፈ፡፡ 8 በአምስተኛው ቀን ለመሄድ ማልዶ ተነሣ፣ ነገር ግን የልጂቱ አባት እንዲህ አለ፣ “ሰውነትህን አበርታ፣ እስከ ማምሻ ድረስ ቆይ አለው፡፡ ስለዚህ ሁለቱም አብረው በሉ፡፡ 9 ሌዋዊው፣ ቁባቱና አገልጋዮቹ ለመሄድ በተነሱ ጊዜ፣ የልጂቱ አባት አማቱ እንዲህ አለው፣ “ተመልከት፣ አሁን ቀኑ እየመሸ ነው፡፡ እባክህ ሌላ ሌሊት በዚህ ቆዩ፣ መልካም ጊዜም ይሁንልህ፡፡ ነገ በማለዳ ተነስታችሁ ወደ ቤታችሁ ተመልሳችሁ መሄድ ትችላላችሁ፡፡” 10 ነገር ግን ሌዋዊው ሌሊቱን በዚያ ለማሳለፍ ፈቃደኛ አልነበረም፡፡ ተነሳና ሄደ፡፡ ኢየሩሳሌምም ወደ ተባለችው ወደ ኢያቡስ ሄደ፡፡ ሁለት የተጫኑ አህዮች ነበሩት፣ ቁባቱም ከእርሱ ጋር ነበረች፡፡ 11 ወደ ኢያቡስም በቀረቡ ጊዜ መሸባቸው፣ አገልጋዩም ለጌታው እንዲህ አለው፣ “ና፣ ወደ ኢያቡሳውያን ከተማ እንሂድና ሌሊቱን በዚያ እናሳልፍ፡፡” 12 ጌታውም፣ “የእስራኤል ሕዝብ ወገን ወዳልሆነ ወደ እንግዳ ሕዝብ ከተማ ውስጥ አንገባም፡፡ እኛ ወደ ጊብዓ እንሄዳለን፡፡” 13 ሌዋዊውም ለወጣቱ ሰው እንዲህ አለው፣ “ና፣ ከእነዚህ ስፍራዎች ወደ አንዱ እንሂድ፣ ሌሊቱንም በጊብዓ ወይም በራማ እናሳልፍ፡፡” 14 ስለዚህ መንገዳቸውን ቀጠሉ፣ የብንያም ነገድ ወደምትሆነው ወደ ጊብዓ ግዛት ሲቀርቡ ፀሐይ ገባችባቸው፡፡ 15 እነርሱም ሌሊቱን በጊብዓ ለማሳለፍ ወደዚያ አቀኑ፡፡ እርሱም ወደ ውስጥ ገባና በከተማው አደባባይ ተቀመጠ፣ ሌሊቱን በዚያ ያሳልፉ ዘንድ ወደ ቤቱ የወሰዳቸው ማንም ሰው አልነበረምና፡፡ 16 ነገር ግን በዚያን ጊዜ አንድ ሽማግሌ ሰው ከእርሻ ሥራው በምሽት እየመጣ ነበር፡፡ እርሱም ከኮረብታማው ከኤፍሬም አገር ነበረ፣ እርሱም በጊብዓ በእንግድነት ተቀምጦ ነበር፡፡ ነገር ግን በዚያ ስፍራ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ብንያማውያን ነበሩ፡፡ 17 እርሱም ዓይኑን አነሳና መንገደኛውን በከተማው አደባባይ አየው፡፡ ሽማግሌውም እንዲህ አለ፣ “ወዴት ትሄዳለህ? ከወዴትስ መጣህ?” 18 ሌዋዊውም እንዲህ አለው፣ “እኛ ከቤተ ልሔም ይሁዳ በጣም ሩቅ ወደሆነው ወደ ኮረብታማው ወደ ኤፍሬም አገር እንሄዳለን፣ እኔም የመጣሁት ከዚያ ነው፡፡ ወደ ቤተ ልሔም ይሁዳ ሄጄ ነበር፣ አሁን ወደ እግዚአብሔር ቤት እየሄድሁ ነው፣ ነገር ግን ወደ ቤቱ የሚወስደኝ ማንም ሰው የለም፡፡ 19 ለአህዮቻችን ገለባና ገፈራ አለን፣ ለእኔና እዚህ ላለችው ለሴት አገልጋይህ፣ ከአገልጋዮችህም ጋር ላለው ለዚህ ወጣት ሰው እንጀራና የወይን ጠጅ አለን፡፡ አንዳችም አላጣንም፡፡” 20 ሽማግሌውም ሰላምታ አቀረበላቸው፣ “ሰላም ለእናንተ ይሁን! የሚያስፈልጋችሁን ሁሉ እኔ እሰጣችኋለሁ፡፡ በአደባባይ ግን ሌሊቱን አትደሩ” አለው፡፡ 21 ስለዚህም ሰውየው ሌዋዊውን ወደ ቤቱ ወሰደው፣ ለአህዮቹም ገፈራ ሰጣቸው፡፡ እግራቸውን ታጠቡ፣ በሉም ጠጡም፡፡ 22 እነርሱም መልካም ጊዜ ነበራቸው፣ ክፉ የሆኑ የከተማይቱ ሰዎች ያደሩበትን ቤት ከበቡ፣ በሩንም ይደበድቡ ነበር፡፡ የቤቱ ባለቤት ለሆነው ለሽማግሌው እንዲህ አሉት፣ “ከእርሱ ጋር መተኛት እንድንችል ወደ ቤትህ የገባውን ሰው አምጣው፡፡” 23 ሰውየውም፣ የቤቱ ባለቤት፣ ወደ እነርሱ ሄደና እንዲህ አላቸው፣ “አይሆንም፣ ወንድሞቼ ሆይ፣ ይህን ክፉ ነገር እባካችሁ አታድርጉ! ይህ ሰው ወደ ቤቴ የገባ እንግዳ ስለሆነ፣ ይህን ክፉ ነገር አትሥሩ፡፡ 24 ተመልከቱ፣ ድንግል ልጄና የእርሱም ቁባት እዚህ አሉ፡፡ አሁን ሄጄ ላምጣቸው፡፡ አስነውሩአቸው፣ የፈለጋችሁትንም አድርጉባቸው፡፡ ነገር ግን በዚህ ሰው ላይ እንደዚህ ያለ ክፉ ነገር አታድርጉበት!” 25 ነገር ግን ሰዎቹ እርሱን አልሰሙትም፣ ስለዚህ ሰውዮው ቁባቱን ያዛትና ወደ ውጭ አወጣላቸው፡፡ እነርሱም ያዟትና ከእርሷ ጋር ተኙ፣ ሌሊቱን በሙሉ አመነዘሩባት፣ ጎህም ሲቀድ ለቀቁአት፡፡ 26 ሴቲቱም በማለዳ መጣችና ጌታዋ ባለበት በሰውዮው ቤት በር ወደቀች፣ ጸሐይ እስኪወጣ ድረስ እዚያው ተዘረረች፡፡ 27 ጌታዋም በማለዳ ተነሣና የቤቱን በር ከፈተ፣ መንገዱንም ለመሄድ ወጣ፡፡ እርሱም ቁባቱ እጅዋን በመድረኩ ላይ ዘርግታ በበሩ ተዘርራ አያት፡፡ 28 ሌዋዊውም እንዲህ አላት፣ “ተነሺ፡፡ እንሂድ፡፡” ነገር ግን ምንም መልስ አልነበረም፡፡ እርሱም በአህያው ላይ ጫናት፣ ተነሥቶም ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ 29 ሌዋዊውም ወደ ቤቱ በመጣ ጊዜ፣ ቢላዋ ወሰደ፣ ቁባቱንም ይዞ ቆራረጣት፣ ብልት በብልት ለአሥራ ሁለት ቈራርጦ ቁራጮቹን ወደ እስራኤል አገር ሁሉ ላከው፡፡ 30 ይህንን ያየ ሁሉ እንዲህ አለ፣ “የእስራኤል ሕዝብ ከግብፅ ምድር ከወጡ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ እንዲህ ያለ ነገር ከቶ አልተደረገም ወይም አልታየም፡፡ ስለ ነገሩ አስቡበት! ምክር ስጡን! ምን ማድረግ እንዳለብን ንገሩን!”



Judges 19:1

በእነዚያ ቀናት

ይህ ሐረግ በታሪክ ፍሰቱ ላይ የሌላ ሁነትን ጅማሬ ያስተዋውቃል። (አዲስ ሁነትን ማስተዋወቅ የሚለውን ተመልከት)

ሩቅ

አብዛኞቹ ሰዎች ከሚኖሩበት የራቀ

ለእርሱ ታማኝ አልነበረችም

ይህ ማለት እርሷ ለግንኙነታቸው ታማኝ አልነበረችምና ከሌሎች ወንዶች ጋር መተኛት ጀምራለች ማለት ነው። አስፈላጊ ከሆነ ይህ በግልጽ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “ከሌሎች ወንዶች ጋር መተኛት ጀመረች”

Judges 19:3

አገልጋዩና ሁለት አህዮች ከእርሱ ጋር ነበሩ

“ከእርሱ ጋር አገልጋዩንና ሁለት አህዮችን ወሰደ”

ዐማቱ፣ የልጅቱ አባት አግባባው

“ዐማቱ፣ ይኸውም የልጅቱ አባት አግባባው” ወይም “የልጅቱ አባት አግባባው”

እንዲቆይ አግባባው

“ስለተናገረው ለመቆየት ወሰነ”

Judges 19:5

አዘጋጀ

ሌዋዊው አዘጋጀ

በቁራሽ እንጀራ ራስህን አበርታ

እዚህ ጋ “እንጀራ” “ምግብ”ን ያመለክታል። አ.ት፡ “ለመጓዝ እንድትበረታ ጥቂት ምግብ ብላ”

ምሽቱን ለማሳለፍ እባክህ ፈቃድህ ይሁን

“እባክህ ደግመህ እደር”

Judges 19:7

ራስህን እያበረታህ እስከ ከሰዓት ቆይ

አማቱ በመብላት ራሱን እንዲያበረታ አሳብ እየሰጠው ነው። ለመሄድ እስከ ከሰዓት እንዲቆይም እየጠየቀው ነው። ይህ በግልጽ መነገር ይችላል። አ.ት፡ “ለመጓዝ እንድትበረታ ጥቂት ምግብ ብላ፤ እስከ ከሰዓት ቆይና ትሄዳለህ” (ፈሊጣዊ አነጋገር እና የሚለውን ተመልከት)

Judges 19:9

አሁን ቀኑ ወደ መምሸቱ ቀርቧል

“ቀኑ እየተገባደደ ነው” ወይም “ምሽት ሊሆን ነው”

Judges 19:10

ይህም ኢየሩሳሌም ነው

“ከጊዜ በኋላ ኢየሩሳሌም ተብላ ተጠርታለች”

የተጫኑ ጥንድ አህዮች ነበሩት

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በሁለቱ አህዮቹ ላይ ኮርቻዎችን ጫነባቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ና፣ እንሂድ

ይህ አሳብ ለመስጠት የሚጠቅም የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ብንሄድ ይሻላል” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ወደ … ጎራ እንበል

ይህ ማለት ጉዟቸውን በመግታት የሆነ ቦታ ላይ እንዲያርፉ ማለት ነው። አ.ት፡ “እዚህ ጋ እንቆይ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 19:12

ወደ … ጎራ እንበል

ይህ ማለት ጉዟቸውን በመግታት የሆነ ቦታ ላይ እንዲያርፉ ማለት ነው። ተመሳሳዩን ሐረግ በመሳፍንት 19፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “እዚህ ጋር እንረፍ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ና፣ እንዲህ እናድርግ

ይህ አሳብ ለመስጠት ጥቅም ላይ የዋለ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “እንድ… አሳብ አቀርባለሁ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 19:14

ጎራ አሉ

ይህ ማለት ጉዟቸውን በመግታት የሆነ ቦታ ላይ እንዲያርፉ ማለት ነው። ተመሳሳዩን ሐረግ በመሳፍንት 19፡11 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት። አ.ት፡ “ቆሙ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በከተማይቱ አደባባይ

ሰዎች ቀን ላይ የሚሰባሰቡበት የገበያ ስፍራ

ወደ ቤቱ ወሰዳቸው

የዚህ ሐረግ ትርጉም አንድ ሰው በቤቱ እንዲያድሩ ጋበዛቸው ማለት ነው። አ.ት፡ “ያንን ሌሊት በቤታቸው እንዲያሳልፉ ጋበዟቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 19:16

ብንያማውያን

ብንያማዊ ሰው የብንያም ተወላጅ ነበር። ይህንን የሕዝብ ወገን ስም በመሳፍንት 3፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ዓይኖቹን አንስቶ

ሰውየው ቀና አለና በዙሪያው ያለውን ተመለከተ። አ.ት፡ “ቀና አለ” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በከተማይቱ አደባባይ

ሰዎች ቀን ላይ የሚሰባሰቡበት የገበያ ስፍራ። ይህንን በመሳፍንት 19፡14 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

Judges 19:18

ወደ ቤቱ የሚወስደኝ ማነው

ይህ ሐረግ የሚያመለክተው ሌሊቱን በዚያ እንዲያሳልፍ ሌላውን ሰው ወደ ቤቱ የሚጋብዝን ሰው ነው። አ.ት፡ “በቤቱ እንዳድር የጋበዘኝ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የሚወስደኝ

እዚህ ጋ ሌዋዊው “እኔ” ይላል፣ ነገር ግን እርሱ እያመለከተ ያለው ራሱን፣ አገልጋዩንና ቁባቱን ጭምር ነው። አ.ት፡ “የሚወስደን”

በዚያ እንጀራና ወይን አለ

ወደ አድራጊ ድምፅ ቀይረው። አ.ት፡ “ብዙ እንጀራና ወይን አለን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ለእኔና ለሴት አገልጋይህ፣ እንዲሁም ከአገልጋይህ ጋር ላለው ለዚህ ወጣት

ሌዋዊው አክብሮቱን ለማሳየት ራሱንና ከእርሱ ጋር ያሉትን ሌሎቹንም በሦስተኛ መደብ አድርጎ ይናገራል። አ.ት፡ “እኔ፣ ቁባቴና አገልጋዬ” (አንደኛ፣ ሁለተኛ ወይም ሦስተኛ መደብ የሚለውን ተመልከት)

የጎደለን ምንም የለም

ይህ አዎንታዊ መግለጫ ሆኖ ሊጻፍ ይችላል። አ.ት፡ “የሚያስፈልገን ሁሉ አለን”

Judges 19:20

ብቻ አትደሩ

“አትደሩ”። “ብቻ” የሚለው ቃል እዚህ ጋ ጥቅም ላይ የዋለው ሌዋዊው እንዲያደርግ ስላልፈለገው ጉዳይ አጽንዖት ለመስጠት ነው።

አደባባይ

ይህ የከተማይቱን አደባባይ ያመለክታል። ይህንን በመሳፍንት 19፡17 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ሌዋዊውን ወደ ቤቱ አመጣው

ይህ ማለት ሌዋዊው በቤቱ እንዲያድር ጋበዘው ማለት ነው። ሌዋዊውን በመጋበዙ ቁባቱንና አገልጋዩንም ደግሞ ጋብዟቸዋል። አ.ት፡ “ሌዋዊውንና አገልጋዮቹን በቤቱ እንዲያድሩ ጋበዛቸው” (የአነጋገር ዘይቤ እና የሚለውን ተመልከት)

Judges 19:22

ልባቸውን ያስደስቱ ነበር

“ልባቸውን ያሰደስቱ” የሚለው ሐረግ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ከአንድ ሰው ጋር ጥሩ ጊዜ ማሳለፍ ማለት ነው። አ.ት፡ “በአንድ ላይ ጥሩ ጊዜ እያሳለፉ ነበር” ወይም “ራሳቸውን ያስደስቱ ነበር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

አንዳንድ ሰዎች -- ቤቱን ከበቡት

አንዳንድ ሰዎች በቤቱ ዙሪያ ቆሙ

Judges 19:24

ተመልከቱ

ይህ ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የሰዎቹን ትኩረት ለማግኘት ነው። አ.ት፡ “አድምጡ”

ሰዎቹ አልሰሙትም

እዚህ ጋ ደራሲው “መስማት” በማለት የሚናገረው ስለ “መስማማት” ነው። አ.ት፡ “ሰዎቹ ግብዣውን አለተቀበሉትም” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ሰውየው ቁባቱን ይዞ

የሰውየው ማንነት አሻሚ ነው። አ.ት፡ “ሌዋዊው ቁባቱን ይዞ”

ማለዳ ላይ

“ፀሐይ በምትወጣበት ጊዜ” ወይም “ንጋት ሲሆን” ይህ ፀሐይ መውጣት የጀመረችበትን ጊዜ ያመለክታል።

ነግቶ ነበር

ይህ ውጪው ብርሃን የሆነበትን ጠዋት ያመለክታል። አ.ት፡ “ፀሐይ ሙሉ በሙሉ ወጥታ ነበር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 19:27

ይሁን እንጂ ምንም ምላሽ አልነበረም

ሴቲቱ ሞታ ስለነበር ምላሽ አልሰጠችም። ይህ በግልጽ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ይሁን እንጂ ሞታ ስለነበር አልመለሰችለትም”

Judges 19:29

የተቆራረጠ አካል

“በክፍል በክፍል”። ደራሲው ይህንን ሥዕላዊ መግለጫ የሚጠቀመው ሌዋዊው አካሏን በተለየ አኳኋን በመቆራረጥ ስላደረገው ነገር አጽንዖት ለመስጠት ነው። “የተቆራረጠ አካል” የአንድን ሰው እጅና እግር ያመለክታል። በቋንቋህ ተመሳሳይ ሐረግ ከሌለ ይህ አገላለጽ ከትርጉምህ ውስጥ መቅረት ይኖርበት ይሆናል። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

አሥራ ሁለት ቁርጥራጭ

“12 ቁርጥራጭ” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ቁርጥራጮቹን በእስራኤል ምድር ወደ ሁሉም ስፍራ ላካቸው

ይህ ማለት የተለያዩ ቁርጥራጮቹን ወደ አሥራ ሁለት የእስራኤል አካባቢዎች ልኳል ማለት ነው። አ.ት፡ “እያንዳንዱን ቁራጭ ወደ ተለያዩ የእስራኤል ክፍሎች ልኳል”


Chapter 20

1 የዚያን ጊዜ የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ እንደ አንድ ሰው ሆነው ወጡ፣ ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ድረስ፣ የገለዓድ አገር ሰዎችንም ጨምሮ፣ በእግዚአብሔር ፊት በምጽጳ ተሰበሰቡ፡፡ 2 የሕዝቡም ሁሉ መሪዎች፣ የእስራኤል ነገዶች ሁሉ፣ እግረኞች ሆነው በሰይፍ የሚዋጉ 400, 000 ሰዎች በእግዚአብሔር ሕዝብ ጉባኤ ውስጥ ስፍራቸውን ያዙ፡፡ 3 በዚህ ጊዜ የእስራኤል ሕዝብ እስከ ምጽጳ ድረስ እንደ ሄዱ የብንያም ሕዝብ ሰሙ፡፡ የእስራኤልም ሕዝብ እንዲህ አሉ፣ “ይህ ክፉ ነገር እንዴት እንደ ተደረገ ንገሩን?” 4 ሌዋዊውም፣ የተገደለችው ሴት ባል፣ እንዲህ ብሎ መለሰ፣ “እኔና ቁባቴ ሌሊቱን በዚያ ለማሳለፍ የብንያም ግዛት ወደሆነችው ወደ ጊብዓ መጣን፡፡ 5 በዚያ ሌሊት የጊብዓ ሰዎች በእኔ ላይ ተነሱ፣ ሊገድሉኝም አስበው ቤቱን ከበቡት፡፡ ቁባቴንም ያዙና ከእርስዋ ጋር ተኙ፣ እርስዋም ሞተች፡፡ 6 እኔም ቁባቴን ወሰድሁና ሰውነቷን ቆራረኋጥኋት፣ ቁርጥራጩንም በእስራኤል ርስት ወደሚገኝ ወደ እያንዳንዱ ክልል ላክሁት፣ ምክንያቱም እንዲህ ዓይነቱን ክፋትና መአት በእስራኤል ላይ ፈጽመዋልና፡፡ 7 አሁንም፣ እናንተ እስራኤላውያን ሁላችሁም ተነጋገሩ፣ ምክራችሁንም ስጡ፣ ለዚህ ነገርም ፍርዳችሁን ስጡ!” 8 ሕዝቡም ሁሉ እንደ አንድ ሰው ሆነው በአንድ ላይ ተነሱ፣ እንዲህም አሉ፣ “ከእኛ ዘንድ ማንም ሰው ወደ ድንኳኑ አይሄድም፣ ማንም ሰው ወደ ቤቱ አይመለስም! 9 ነገር ግን አሁንም በጊብዓ ላይ ማድረግ ያለብን ነገር ይህ ነው፡- ዕጣው እንደሚመራን እንወጋታለን፡፡ 10 ከእስራኤል ነገዶች በሙሉ ለሕዝቡ ስንቅ እንዲይዙ ከመቶው አስር ሰው፣ ከሺህ መቶ ሰው፣ ከአስር ሺህ አንድ ሺህ ሰው እንወስዳለን፣ ይህም ሕዝቡ ወደ ብንያም ጊብዓ በሚመጣበት ጊዜ እነርሱ በእስራኤል ላይ ለፈጸሙት ክፋት ይቀጧቸው ዘንድ ነው፡፡” 11 ስለዚህም የእስራኤል ወታደሮች በሙሉ በአንድ ዓላማ በመስማማት በከተማይቱ ላይ ለመዝመት ተሰበሰቡ፡፡ 12 የእስራኤልም ነገዶች ወደ ብንያም ነገድ ሁሉ እንዲህ ብለው ሰዎችን ላኩ፣ “በእናንተ መካከል የተደረገው ይህ ክፉ ነገር ምንድር ነው? 13 ስለዚህ እንድንገድላቸውና ይህንን ክፋት ከእስራኤል ሙሉ ለሙሉ ለማስወገድ በጊብዓ ውስጥ ያሉትን እነዚህን ክፉ ሰዎች አውጥታችሁ ስጡን፡፡” ነገር ግን ብንያማውያን የወንድሞቻቸውን የእስራኤልን ሕዝብ ቃል አልሰሙም፡፡ 14 የዚያን ጊዜ የብንያም ሕዝብ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ለመዋጋት ዝግጅት ያደርጉ ዘንድ ከየከተማው ወጥተው ወደ ጊብዓ ተሰበሰቡ፡፡ 15 የብንያም ሕዝብ ከየከተማው በአንድ ላይ ለመዋጋት መጡ፣ በዚያም ቀን በሰይፍ ስለት ለመዋጋት የሰለጠኑ 26, 000 ወታደሮች ነበሩ፤ ከዚህ በተጨማሪ ከጊብዓ ነዋሪዎች ሰባት መቶ የተመረጡ ሰዎች ተቈጠሩ፡፡ 16 ከእነዚህ ወታደሮች መካከል ሰባት መቶ የተመረጡ ግራኝ ሰዎች ነበሩ፤ እያንዳንዳቸውም ድንጋይ ወንጭፈው አንዲት ጠጕርስ እንኳ አይስቱም፡፡ 17 የእስራኤል ወታደሮች፣ ከብንያም ወገን የሆኑትን ሳይጨምር፣ በሰይፍ ስለት ለመዋጋት የሰለጠኑ አራት መቶ ሺህ ሰዎች ተቆጠሩ፡፡ እነዚህ በሙሉ የጦር ሰዎች ነበሩ፡፡ 18 የእስራኤልም ሕዝብ ተነሱ፣ ወደ ቤቴል ወጡ፣ ከእግዚአብሔርም ምክር ጠየቁ፡፡ እንዲህም ብለው ጠየቁ፣ “የብንያምን ልጆች ለመውጋት ለእኛ መጀመርያ ማን ይውጣልን?” እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፣ “ይሁዳ በመጀመርያ ይዋጋል፡፡” 19 የእስራኤልም ሕዝብ በማለዳ ተነሱና በጊብዓ ፊት ለውጊያ ተዘጋጁ፡፡ 20 የእስራኤልም ወታደሮች ከብንያም ጋር ለመዋጋት ወጡ፡፡ እነርሱም በጊብዓ ከእነርሱ ጋር ለመዋጋት ቦታ ቦታቸውን ይዘው ተሰለፉ፡፡ 21 የብንያም ወታደሮች ከጊብዓ ወጥተው መጡ፣ በዚያም ቀን ከእስራኤላውያን ሰራዊት 22, 000 ሰዎች ገደሉ፡፡ 22 ነገር ግን የእስራኤል ወታደሮች ራሳቸውን አበረቱ፣ በመጀመርያው ቀን ተሰልፈው በነበረበት ስፍራ ላይ እንደገና ቦታ ቦታቸውን በመያዝ የውጊያውን መስመር አዘጋጁ፡፡ 23 የእስራኤልም ሕዝብ ወደ ላይ ወጡና እስከ ማታ ድረስ በእግዚአብሔር ፊት አለቀሱ፡፡ከእግዚአብሔርም ምሪትን ፈለጉ እንዲህም ብለው ጠየቁ፣ “ከወንድሞቻችን ከብንያም ሕዝብ ጋር ለመዋጋት እንደገና ወደዚያ መቅረብ ይገባናልን?” እግዚአብሔርም “በእነርሱ ላይ ውጡና ግጠሟቸው” አለ፡፡ 24 ስለዚህም በሁለተኛው ቀን የእስራኤል ወታደሮች የብንያምን ወታደሮች ለመዋጋት ሄዱ፡፡ 25 በሁለተኛው ቀን የብንያም ወታደሮች ከጊብዓ እነርሱን ሊወጉ ወጡና ከእስራኤል ወታደሮች 18, 000 ሰዎች ገደሉ፡፡ እነዚህም ሰዎች ሁሉ በሰይፍ ለመዋጋት የሰለጠኑ ነበሩ፡፡ 26 የዚያን ጊዜ የእስራኤል ወታደሮች ሁሉ፣ ሕዝቡም ሁሉ ወደ ቤቴል ወጡና አለቀሱ፣ በዚያም በእግዚአብሔር ፊት ተቀመጡ፣ እነርሱም በዚያ ቀን እስከ ምሽት ድረስ ጾሙ፣ በእግዚአብሔር ፊት የሚቃጠል መሥዋዕትና የሰላም መሥዋዕት አቀረቡ፡፡ 27 የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሔርን ጠየቁ፣ በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ታቦት በዚያ ነበረ፣ 28 በእነዚህ ጊዜያቶች የአሮን ልጅ የአልዓዛር ልጅ ፊንሐስ በታቦቱ ፊት ያገለግል ነበር፣ “ከወንድሞቻችን ከብንያም ሕዝብ ጋር አንድ ጊዜ ለመዋጋት እንደገና እንሂድ ወይስ እንቅር?” እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፣ “ጥቃት ፈጽሙባቸው፣ ነገ እነርሱን እንድታሸንፉ እረዳችኋለሁና፡፡” 29 ስለዚህ እስራኤል በጊብዓ ዙሪያ በምስጢራዊ ስፍራዎች የተደበቁ ሰዎች አኖሩ፡፡ 30 የእስራኤል ወታደሮች ከብንያም ወታደሮች ጋር ለሦስተኛ ቀን ተዋጉ፣ ከዚህ በፊት እንዳደረጉት በጊብዓ ላይ የውጊያ መስመራቸውን ዘርግተው ተሰለፉ፡፡ 31 የብንያምም ሕዝብ ሄዱና ሕዝቡን ተዋጉ፣ ከከተማይቱም እንዲወጡ ተደረጉ፡፡ ከሕዝቡም አንዳንዶቹን መግደል ጀመሩ፡፡ ከእስራኤልም ወገን የሞቱ ሠላሳ የሚያህሉ ሰዎች በእርሻዎቹና በመንገዶቹ ነበሩ፣ ከመንገዶቹ አንዱ ወደ ቤቴል የሚወስድ ነው፣ ሌላኛው ደግሞ ወደ ጊብዓ የሚወስድ ነው፡፡ 32 የዚን ጊዜ የብንያምም ሕዝብ እንዲህ አሉ፣ “እንደ በፊቱ ተሸንፈዋል፣ ከእኛ እየሸሹ ነው፡፡” ነገር ግን የእስራኤል ወታደሮች እንዲህ አሉ፣ “እንሽሽ፣ ከከተማይቱ እንዲወጡና ወደ መንገዶቹ እንዲሄዱ እናድርጋቸው፡፡” 33 የእስራኤልም ወታደሮች በሙሉ ከስፍራቸው ተነሱና በበኣልታማር ለውጊያ ራሳቸውን አዘጋጅተው ተሰለፉ፡፡ በምስጢራዊ ስፍራ ተደብቀው የነበሩት የእስራኤል ወታደሮችም ከነበሩበት ስፍራ ከጊብዓ ወጥተው ሮጡ፡፡ 34 ከእስራኤልም ሁሉ 10, 000 የተመረጡ ሰዎች በጊብዓ ላይ መጡ፣ ጦርነቱም በርትቶ ነበር፣ ነገር ግን ብንያማውያን ጥፋት ወደ እነርሱ ቀርቦ እንደነበር አላወቁም፡፡ 35 እግዚአብሔርም ብንያምን በእስራኤል ፊት ድል አደረገ፡፡ በዚያም ቀን የእስራኤል ወታደሮች 25, 100 የብንያም ሰዎችን ገደሉ፡፡ የሞቱት ሰዎች በሙሉ በሰይፍ ለመዋጋት ስልጠና የወሰዱ ነበሩ፡፡ 36 ስለዚህ የብንያም ወታደሮች እንደ ተሸነፉ አዩ፡፡ የእስራኤልም ሰዎች ለብንያም ስፍራ ለቀቁላቸው፣ ምክንያቱም ከጊብዓ ውጭ በድብቅ ስፍራዎች ባስቀመጡአቸው ሰዎች ላይ ተማምነው ነበርና፡፡ 37 የዚያን ጊዜ ተደብቀው የነበሩት ሰዎች ተነሱና ፈጥነው ወደ ጊብዓ ሮጡ፣ በከተማይቱም ውስጥ የሚኖረውን ሰው በሙሉ በሰይፋቸው ገደሉ፡፡ 38 በእስራኤል ወታደሮችና በምስጢር በተደበቁት ሰዎች መካከል ከከተማው የታላቅ ጢስ ደመና በምልክትነት እንዲያስነሡ ስምምነት ተደርጎ ነበር፡፡ 39 የእስራኤልም ወታደሮች በውጊያው ጊዜ ከጦርነቱ ርቀው እንዲያፈገፍጉ ነበር፡፡ የዚያን ጊዜ ብንያማውያን ማጥቃት ጀመሩ ሠላሳ የእስራኤልንም ሰዎች ገደሉ፣ እነርሱም እንዲህ አሉ፣ “እንደ መጀመርያው የጦርነት ጊዜ በእኛ ፊት መሸነፋቸው እርግጠኛ ነው፡፡” 40 ነገር ግን የጢሱ ዓምድ ከከተማው ወደ ላይ መውጣት በጀመረ ጊዜ፣ ብንያማውያን ወደ ኋላቸው ሲመለከቱ ጢሱ ከከተማዋ በሙሉ ወደ ሰማይ ሲወጣ አዩ፡፡ 41 የዚያን ጊዜ የእስራኤል ወታደሮች ዞረው አጠቋቸው፡፡ የብንያም ሰዎችም ደነገጡ፣ በእነርሱ ላይ ጥፋት እንደመጣባቸው አይተዋልና፡፡ 42 ስለዚህ ከእስራኤል ወታደሮች ተመልሰው ወደ ምድረ በዳው መንገድ ሸሹ፡፡ ነገር ግን ውጊያው ተከታትሎ ደረሰባቸው፡፡ የእስራኤልም ወታደሮች ከከተማዎቹ ወጡና በቆሙበት ስፍራ ገደሉአቸው፡፡ 43 እነርሱም ብንያማውያንን ከበቡና ተከትለዋቸው ሄዱ፤ በመኑሔም አሸነፉአቸው፣ ከጊብዓ በስተ ምሥራቅ በኩል እስካለው ስፍራ ድረስ አሳደዱአቸው፡፡ 44 ከብንያም ነገድም 18, 000 ወታደሮች ሞቱ፣ እነዚህ ሰዎች በሙሉ በጦርነት ምርጥ ተዋጊዎች ነበሩ፡፡ 45 እነርሱም ተመልሰው በምድረ በዳ ወዳለው ወደ ሬሞን ዓለት ሸሹ፡፡ እስራኤላውያንም ከእነርሱ ተጨማሪ አምስት ሺህ ሰዎችን በየመንገዱ ገደሉ፡፡ እነርሱም ተከታተሉአቸው፣ ወደ ጊድአምም በቅርብ እየተከታተሉአቸው ተጨማሪ ሁለት ሺህ ሰዎችን ገደሉ፡፡ 46 በዚያ ቀን የሞቱት የቢኒያም ወታደሮች በሙሉ 25, 000 በሰይፍ ለመዋጋት ልዩ ስልጠና የወሰዱ ሰዎች ነበሩ፤ እነዚህ በሙሉ በጦርነት ምርጥ ተዋጊዎች ነበሩ፡፡ 47 ነገር ግን ስድስት መቶ ሰዎች ተመልሰው በምድረ በዳ ወዳለው ወደ ሬሞን ዓለት ሸሹ፡፡ ለአራት ወራት ያህል በሬሞን ዓለት ተቀመጡ፡፡ 48 የእስራኤልም ወታደሮች በብንያም ሕዝብ ላይ እንደገና ተመለሱ፣ ሞላውን ከተማ፣ ከብቶችንና ያገኙትንም ሁሉ አጠቁ ደግሞም ገደሉ፡፡ በመንገዳቸው ያገኙትን ማንኛውንም ከተማ ሁሉ በእሳት አቃጠሉ፡፡



Judges 20:1

እንደ አንድ ሰው

ይህ ንጽጽር የሚናገረው አንድ ቡድን እንደ አንድ ሰው መንቀሳቀሱን ነው። ይህ የሚያመለክተው በቡድን የሆኑ ሰዎች በተመሳሳይ መንገድ ሁሉንም ነገር በጋራ የሚያደርጉ መሆናቸውን ነው። አ.ት፡ “አንድ ሰው የሆኑ ያህል” (ንጽጽር የሚለውን ተመልከት)

ከዳን እስከ ቤርሳቤህ

ይህ በጥቅሉ ምድሪቱን ያመለክታል። አ.ት፡ “ከአሥራ አንዱ ነገዶች በሙሉ”

እግዚአብሔር -- 400,000 እግረኛ ሰዎች

“እግዚአብሔርና በተጨማሪም 400,000 መደበኛ ወታደሮች መጡ”

ለውጊያ የተዘጋጁ

“ወደ ጦርነት ለመሄድ ብቁ የሆኑ”። የሚሄዱት እርስ በእርስ ለመዋጋት አልነበረም።

Judges 20:3

አሁን

ይህ ቃል ጥቅም ላይ የዋለው ዋናው የትረካ መስመር ለአፍታ መገታቱን ለማሳየት ነው። እዚህ ጋ የመጽሐፉ ደራሲ የብንያም ሰዎች ስለሚያውቁት ነገር ዳራዊ መረጃ ይናገራል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ወደ ምጽጳ ወጥተው ነበር

ምጽጳ የምትገኘው ከፍ ባሉት ተራራዎች ላይ ነበር።

ሌሊቱን ለማሳለፍ

“ለሌሊቱ” ወይም “አንድ ሌሊት ለማደር”

Judges 20:5

ክፋትና የጭካኔ ተግባር

“የጭካኔ ተግባር” የሚለው ቃል “ክፋት”ን ያብራራዋል። አ.ት፡ “አሰቃቂ ክፋት”

አሁን

ይህ ቃል ጥቅም ላይ የዋለው የሌዋዊውን ንግግር መደምደሚያ ለማስተዋወቅ ነው።

እዚህ ላይ አስተያየትና ምክራችሁን ስጡ

“አስተያየት” እና “ምክር” የሚሉት ቃላት የሚያመለክቱት አንድን ነገር ሲሆን አጽንዖት ለመስጠት ተደግመዋል። ሁለቱ ሊጣመሩ ይችላሉ። አ.ት፡ “ስለዚህ ጉዳይ ምን ማድረግ እንደሚኖርብን ወስኑ”

Judges 20:8

እንደ አንድ

ይህ ንጽጽር የሚናገረው እንደ አንድ ሰው ስለሚንቀሳቀስ ቡድን ነው። ሁሉም በተመሳሳይ መንገድ በአንድ ላይ ተንቀሳቀሱ። አ.ት፡ “አንድ ሰው የሆኑ ያህል” (ንጽጽር የሚለውን ተመልከት)

ከእኛ ማንም ወደ ድንኳኑ አይሄድም … ከእኛ ማንም ወደ ቤቱ አይመለስም

እነዚህ ሁለት አንቀጾች ስለ አንድ ነገር ሁለቴ መናገራቸው በመሠረቱ አጽንዖት ለመስጠት ነው። ሊጣመሩ ይችላሉ። “ማንም . . . አይሄድም” እና “ማንም . . . አይመለስም” የሚሉት ቃላት ሰዎቹ በዚያ መቆየታቸውን እንዴት እንደሚቀጥሉ አጽንዖት ይሰጣል። በአዎንታዊ ድምፅ ሊነገሩ ይችላሉ። አ.ት፡ “ሁላችንም እዚሁ እንቆያለን”

አሁን ግን

እነዚህ ቃላት ሰዎቹ ከመጀመሪያው ጩኸት በኋላ የተናገሩትን ዐቢይ ጉዳይ ያስተዋውቃሉ።

ዕጣው እንደ መራቸው

እግዚአብሔር የሚፈልገውን ለማወቅ ምልክት የተደረገባቸውን ጠጠሮች መወርወርን ወይም ማንከባለልን ያካትታል።

Judges 20:10

ከመቶ ሰዎች አሥሩ . . . ከሺህ አንድ መቶ . . . ከአሥር ሺ አንድ ሺ

“ከ100 ሰው 10፣ ከ1,000 ሰው 100፣ ከ10,000 ሰው 1,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

አቅርቦቶች

ሰዎቹ የሚያስፈልጋቸው ምግብና ሌሎች ነገሮች

በከተማይቱ ላይ ተሰበሰቡ

“ከተማይቱን ለመውጋት በአንድ ላይ ተሰበሰቡ”

Judges 20:12

ለሞት አብቋቸው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ነው። አ.ት፡ “ግደሏቸው” ወይም “አስወግዷቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

የወንድሞቻቸው ድምፅ

እዚህ ጋ “ድምፅ” የሚያመለክተው የተናገሩትን መልዕክታቸውን ነው። አ.ት፡ “ወንድሞቻቸው የተናገሩትን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:15

ሃያ ስድስት ሺህ

“26,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ሰባት መቶ

“700” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ግራኝ

ግራኝ የሆነ ሰው ከቀኝ እጃቸው ይልቅ በግራ እጃቸው የበለጠ መሥራት ከሚችሉ ሰዎች አንዱ ነው።

ድንጋይ በማስወንጨፍ ጸጉር የማይስቱ

ይህ የሚያመለክተው በሚያስደንቅ ሁኔታ ዒላማቸውን የሚመቱ መሆናቸውን ነው። ይህ በአዎንታዊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በጸጉር ላይ እንኳን ድንጋይ ወርውረው መምታት ይችላሉ” ወይም “እንደ ጸጉር በቀጠነ ነገር ላይ ድንጋይ ወርውረው መምታት ይችላሉ”

Judges 20:17

ሳይቆጠሩ

“ሳይጨመሩ”

400,000

“አራት መቶ ሺህ ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የእግዚአብሔርን ምሪት

“ምን ማድረግ እንዳለባቸው እግዚአብሔርን ጠየቁ” ወይም “እንዴት መቀጠል እንዳለባቸው እግዚአብሔርን ጠየቁ”

Judges 20:19

ሠፈራቸውን ወደ ጊብዓ አዛወሩ

ስለ ዕብራይስጡ ጽሑፍ ትርጓሜ አንዳንድ ጥያቄዎች አሉ። ሠፈራቸውን በጊብዓ አቅራቢያ አደረጉ ከሚለው ትርጉም ይልቅ ሰራዊቱ ተጉዞ በጊብዓ ትይዩ ለጦርነት ተዘጋጅተው ቆሙ ማለት ይሆናል።

ሃያ ሁለት ሺህ

“22,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:22

ራሳቸውን አበረታቱ

እዚህ ጋ “አበረታቱ” የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን እርስ በእርሳቸው ተበረታቱ ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ለጦርነት ተሰለፉ

ይህ ምናልባት እስራኤላውያኑ በመሰለፍ ለቀጣዩ ቀን ጦርነት ተዘጋጅተዋል ማለት ሊሆን ይችላል። አ.ት፡ “በቀጣዩ ቀን ለመዋጋት ተዘጋጁ”

ከእግዚአብሔር ምሪት ፈለጉ

እንዴት ባለ መንገድ እንደ ፈለጉ አልተገለጸም። ምናልባት ካህኑ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ ዕጣ ጥሎ ይሆናል።

Judges 20:24

አሥራ ስምንት ሺህ

“18,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:26

በእግዚአብሔር ፊት

“በእግዚአብሔር ሀልዎት” ወይም “ለእግዚአብሔር”

Judges 20:27

የእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ታቦት . . . በእነዚያ ቀናት በታቦቱ ፊት ያገለግል ነበር

ይህ አንባቢው፣ ሕዝቡ እግዚአብሔር ምላሽ እንዲሰጣቸው እንዴት እንደጠየቁ መገንዘብ እንዲችል ለመርዳት ደራሲው የጨመረው ዳራዊ መረጃ ነው። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

በእነዚያ ቀናት በዚያ ነበር

“በእነዚያ ቀናት በቤቴል ነበር”

በታቦቱ ፊት ያገለግል ነበር

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “በታቦቱ ፊት በክህነት ያገለግል ነበር”

ማጥቃት

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የብንያምን ሰራዊት አጥቁ”

Judges 20:29

እስራኤል ሰዎቹን ቦታ አስያዙ

እዚህ ጋ “እስራኤል” የሚያመለክተው የእስራኤልን ሕዝብ ነው። አ.ት፡ “ እስራኤላውያን” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ድብቅ ቦታዎች

“በደፈጣ”

Judges 20:31

ከሰዎቹ ጋር ተዋጉ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከእስራኤል ሰዎች ጋር ተዋጉ”

ከከተማይቱ ተስበው ወጡ

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “የእስራኤል ሰዎች ከከተማይቱ ስበው አወጧቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከሰዎቹ ጥቂቶቹን መግደል ጀመሩ

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “የብንያም ሰዎች ከእስራኤል ሰዎች ጥቂቶቹን መግደል ጀመሩ”

Judges 20:32

ልክ እንደ መጀመሪያው

“ልክ እንደ ቀድሞው” ወይም “ልክ እንደ መጀመሪያዎቹ ሁለት ጊዜያት”

በኣል ታማር

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ማሬህ ጊብዓ

ይህ የአንድ ቦታ ስም ነው። ሌሎች ትርጉሞች ምናልባት “የጊብዓ ሜዳዎች” ወይም “ከጊብዓ በስተምዕራብ” ወይም “ማሬህ ጌባ” (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:34

አሥር ሺህ

“10,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የተመረጡ ሰዎች

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን እነዚህ በተለየ ሁኔታ ጥሩ ወታደሮች ነበሩ ማለት ነው። አ.ት፡ “በሚገባ የሰለጠኑ ወታደሮች” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

ጥፋታቸው እንደ ቀረበ

እዚህ ጋ የጥፋት መቅረብ አጠገባቸው እንደ ቆመ ያህል ተደርጎ ተነግሯል። አ.ት፡ “ወዲያውኑ ፈጽሞ ሊሸነፉ ነው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

25,100 ሰዎች

“ሃያ አምስት ሺህ አንድ መቶ ሰዎች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:36

የእስራኤል ሰዎች ከጊብዓ ውጪ . . . ባሉት ሰዎች ስለተማመኑ ለብንያም ሰዎች አፈገፈጉላቸው

ከዚህ ዐረፍተ ነገር እስከ ቁጥር 41 መጨረሻ ድረስ ያለው የደፈጣ ተዋጊዎቹ ብንያማውያንን እንዴት እንዳሸነፏቸው ጸሐፊው ለአንባቢያን ለማብራራት የጨመረው ዳራዊ መረጃ ነው።

ለብንያማውያን አፈገፈጉላቸው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን ሆን ብለው ወደ ኋላ ተመልሰዋል ማለት ነው። አ.ት፡ “ብንያማውያን ወደ ፊት እንዲመጡ ፈቅደውላቸው ነበር” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

በሰዎቹ ተማምነው ነበር

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን በሰዎቻቸው ታምነዋል ማለት ነው። (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:39

ከጦርነቱ የሚመለሱ

“ከጦርነቱ የሚያፈገፍጉ”

በፊታችን ተሸንፈዋል

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “አሸንፈናቸዋል” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:40

ጥፋት

ታላቅ ጉዳት፣ መከራ፣ ስቃይ

መጡባቸው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ ደረሰባቸው ማለት ነው። አ.ት፡ “ደረሰባቸው” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:42

ነገር ግን በጦርነቱ ድል ተደረጉ

ይህ አንድ ሰው ሌላውን በሚይዝበት መልኩ የተነገረው ስለ ጦርነት ነው። አ.ት፡ “ነገር ግን የእስራኤል ወታደሮች ያዟቸው” ወይም “ነገር ግን ከጦርነቱ ለማምለጥ አልቻሉም” (ሰውኛ የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:43

ኖሃህ

ይህ የአንድ የቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ጨፈጨፏቸው

የብንያማውያን መደምሰስ እስራኤላውያን በሬሳዎቻቸው ላይ እንደተረማመዱ ሆኖ ተነግሯል። አ.ት፡ “ሙሉ በሙሉ ደመሰሷቸው” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

አሥራ ስምንት ሺህ

“18,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በጦርነት የታወቁ ነበሩ

“በጦርነት ውስጥ በጀግንነት የተዋጉ ነበሩ”

Judges 20:45

ተመልሰው ሸሹ

“የቀሩት ብንያማውያን ተመልሰው ሸሹ”

አምስት ሺህ … ሁለት ሺህ

“5,000 … 2,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

ጊዶም

ይህ የአንድ ቦታ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሃያ አምስት ሺህ

“25,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 20:47

ስድስት መቶ

“600” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

በብንያም ሰዎች ላይ ተመለሱባቸው

እነዚህ ወደ ሬሞን ዐለት የሸሹት የብንያም ሰዎች ወታደሮች ሳይሆኑ ገና በከተማው ውስጥ የነበሩት ናቸው።

ከተማው

እዚህ ጋ “ከተማው” የሚያመለክተው በዚያ ከተማ የሚኖሩትን ሰዎች ነው። አ.ት፡ “በከተማው የነበረው ሁሉ” (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

በመንገዳቸው

ይህ የአነጋገር ዘይቤ የሚያመለክተው ወደ ከተማይቱ በሚሄዱበት ጊዜ ያገኙትን ነገር ሁሉ ነው። አ.ት፡ “ወደ … መጡ” (የአነጋገር ዘይቤ የሚለውን ተመልከት)


Chapter 21

1 በዚያን ጊዜ የእስራኤል ወታደሮች በምጽጳ “ከእኛ ማንም ሰው ሴት ልጁን በጋብቻ ለብንያማውያን መዳር የለበትም” በማለት ቃል ገብተው ነበር፡፡ 2 ከዚያም ሕዝቡ ወደ ቤቴል ሄዱና በዚያ በእግዚአብሔር ፊት እስከ ምሽቱ ድረስ ተቀመጡ፣ ድምፃቸውንም ከፍ በማድረግ አምርረው አለቀሱ፡፡ 3 እነርሱም እንዲህ ሲሉ ጮኹ፣ “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፣ ይህ በእስራኤል ለምን ሆነ? ዛሬ ከእኛ አንዱ ነገድ መታጣቱ ለምንድን ነው?” 4 በሚቀጥለውም ቀን ሕዝቡ በጠዋት ተነሡና በዚያ መሠዊያ ሠሩ፣ የሚቃጠልና የሰላም መሥዋዕትንም አቀረቡ፡፡ 5 የእስራኤልም ሕዝብ እንዲህ አሉ፣ “ከእስራኤል ነገዶች በሙሉ ወደ እግዚአብሔር ጉባኤ ያልመጣ የትኛው ነው?” በምጽጳ ወደ እግዚአብሔር ፊት ስላልመጣ ማንም ሰው በጣም ወሳኝ የሆነ ቃል ኪዳን አድርገው ነበርና፡፡ እነርሱም እንዲህ አሉ፣ “እርሱ ፈጽሞ ሊገደል ይገባዋል፡፡” 6 የእስራኤልም ሕዝብ ስለ ወንድማቸው ስለ ብንያም አዘኑ፡፡ አነርሱም እንዲህ አሉ፣ “ዛሬ ከእስራኤል ነገድ አንዱ ተቆርጧል፡፡ 7 ሴቶች ልጆቻችንን ከእነርሱ ለአንዳቸውም ቢሆን በጋብቻ ላንሰጥ ለእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ስለገባን ለተረፉት ሚስቶችን የሚሰጣቸው ማን ነው?” 8 እነርሱም አሉ፣ “ከእስራኤል ነገድ በምጽጳ ወደ እግዚአብሔር ያልመጣ የትኛው ነው?” ከኢያቢስ ገለዓድ ወደ ጉባኤው አንድም ሰው አለመምጣቱን አወቁ፡፡ 9 ሕዝቡም በቅደም ተከተል ተሰልፈው እንዲቆጠሩ በተደረገ ጊዜ፣ እነሆ፣ ከኢያቢስ ገለዓድ ነዋሪዎች ማንም ሰው በዚያ አልነበረም፡፡ 10 ጉባኤውም 12, 000 ኃያላን ሰዎችን ወደ ኢያቢስ ገለዓድ ልከው በዚያ ያሉትን ሰዎች ሴቶችንና ሕፃናትንም ጭምር ጥቃት እንዲያደርሱባቸውና እንዲገድሏቸው አዘዙአቸው፡፡ 11 “እንግዲህ የምታደርጉት ይህ ነው፡- ወንዱን በሙሉ እንዲሁም ከወንድ ጋር የተኛችውንም ሴት በሙሉ ግደሉ፡፡” 12 ሰዎቹም በኢያቢስ ገለዓድ ከሚኖሩት መካከል ከወንድ ጋር ተኝተው የማያውቁ አራት መቶ ወጣት ሴቶች አገኙ፣ እነርሱንም በከነዓን ወዳለው በሴሎ ወደሚገኘው ሰፈር ወሰዷቸው፡፡ 13 ጉባኤውም በሙሉ መልክት ላኩ፣ በሬሞን ዓለት ለነበሩት ለብንያም ሕዝብ የሰላም ጥሪ እንዳቀረቡላቸውም ነገሩአቸው፡፡ 14 ሲለዚህ በዚያን ጊዜ ብንያማውያን ተመለሱ፣ የኢያቢስ ገለዓድንም ሴቶች ሰጧቸው፡፡ ነገር ግን ለሁሉም የሚበቁ ሴቶች አልነበሩም፡፡ 15 ሕዝቡም በብንያም ላይ በሆነው ገር አዘኑ፣ ምክንያቱም እግዚአብሔር በእስራኤል ነገዶች መካከል ስብራት አድርጓልና፡፡ 16 የዚያን ጊዜ የጉባኤው መሪዎች እንዲህ አሉ፣ “የብንያም ሴቶች ተገድለዋልና፣ ለተረፉት ብንያማውያን ሚስቶችን እንዴት እናግኝላቸው?” 17 እንዲህም አሉ፣ “ከእስራኤል አንድ ነገድ እንዳይጠፋ ከብንያም አሁን በሕይወት ላሉት ሰዎች ርስት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ 18 ከሴቶች ልጆቻችን ሚስቶች ልንሰጣቸው አንችልም፡፡ የእስራኤል ሕዝብ፣ ‘ለብንያም ሚስት የሚሰጥ ርጉም ይሁን’ የሚል ቃል ኪዳን ገብተው ነበርና፡፡” 19 ስለዚህ እንዲህ አሉ፣ “በቤቴል በሰሜን በኩል፣ ከቤቴልም ወደ ሴኬም በሚወስደው መንገድ በምሥራቅ በኩል፣ በለቦና በደቡብ በኩል ባለችው በሴሎ በየዓመቱ የእግዚአብሔር በዓል እንዳለ ታውቃላችሁ፡፡” 20 እነርሱም ለብንያም ሰዎች እንዲህ ብለው አዘዙአቸው፣ “ሂዱና በምስጢር ተሸሸጉ፣ በወይኑ ስፍራም ተደበቁ፡፡ 21 የሴሎ ልጃገረዶች ለመጨፈር የሚወጡበትን ጊዜ ተመለክቱ፣ የዚያን ጊዜ ከወይኑ ስፍራ ፈጥናችሁ ውጡና እያንዳንዳችሁ ከሴሎ ልጃገረዶች ለየራሳችሁ ሚስት ውሰዱ፣ ከዚያም ወደ ብንያም ምድር ተመለሱ፡፡ 22 አባቶቻቸው ወይም ወንድሞቻቸው ሊጣሉን በመጡ ጊዜ፣ እንዲህ እንላቸዋለን፣ ‘ምህረት አድርጉልን! ባልና ሚስት ሆነው ይጽኑ ምክንያቱም በጦርነቱ ጊዜ እኛ ለያንዳንዳቸው ሚስት አላገኘንላቸውም፡፡ እናተ ደግሞ ሴቶች ልጆቻችሁን ለእነርሱ ስላልሰጣችሁ፣ ቃል ኪዳኑን በተመለከተ በደለኞች አይደላችሁም፡፡’” 23 የብንያምም ሕዝብ እንዲሁ አደረጉ፣ በቍጥራቸው መጠን የሚያስፈልጋቸውን ያህል ሚስቶች ይጨፍሩ ከነበሩት ልጃገረዶች ወሰዱ፣ ሚስትም ይሆኗቸው ዘንድ ይዘዋቸው ሄዱ፡፡ እነርሱም ወደ ርስታቸው ስፍራ ተመልሰው ሄዱ፤ ከተሞችንም እንደገና ሠሩ፣ በውስጣቸውም ኖሩ፡፡ 24 በዚያን ጊዜ የእስራኤል ሕዝብ ያን ስፍራ ለቀቁና ወደ ቤታቸው ሄዱ፣ እያንዳንዱም ወደ ነገዱና ወደ ወገኑ ሄደ፣ እያንዳንዱም ወደ ርስቱ ተመለሰ፡፡ 25 በዚያም ዘመን በእስራኤል ውስጥ ንጉሥ አልነበረም፡፡ እያንዳንዱ ሰው በዓይኖቹ ፊት መልካም መስሎ የታየውን ያደርግ ነበር፡፡



Judges 21:1

የእስራኤል ሰዎች ከብንያማውያን ጋር እንዳይጋቡ ቃል ኪዳን ገብተው ነበር

ይህ ዳራዊ መረጃ እስራኤላውያን ከብንያማውያን ጋር ከመዋጋታቸው በፊት ስላደረጉት ቃል ኪዳን ለአንባቢው ይናገራል። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ብንያማውያን

ይህ የብንያም ተወላጆች ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 3፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፣ ዛሬ ከነገዶቻችን አንዱን አጥተናልና ይህ ለምን በእስራኤል ላይ ሆነ?

የእስራኤል ሰዎች ይህንን ምላሽ የማይፈልግ ጥያቄ የተጠቀሙት ጥልቅ ሐዘናቸውን ለመግለጽ ነው። ይህ ጥያቄ እንደ መግለጫ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “እግዚአብሔር ሆይ፣ ከእስራኤል ነገዶች አንዱ ሙሉ በሙሉ በመጥፋቱ በጣም አዝነናል” (ምላሽ የማይሻ ጥያቄ የሚለውን ተመልከት)

Judges 21:4

እስራኤላውያኑ፣ “ከእስራኤል ነገዶች ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ጉባዔ ያልመጣው የትኛው ነው?” አሉ

ሰዎቹ ብንያማውያንን ከመውጋታቸው በፊት በምጽጳ እያሉ የእስራኤላውያኑ ጉባዔ የተናገሩትን ያመለክታል።

በምጽጳ ወደ እግዚአብሔር ያልመጣውን ማንንም ቢሆን የሚመለከት አስፈላጊ የሆነ መሐላ አድርገው ነበር፤ እንዲህ አሉ፣ “እርሱ በእርግጥ መሞት ይገባዋል”።

ይህ እስራኤላውያኑ ብንያማውያኑን ከመውጋታቸው በፊት በምጽጳ ስላደረጉት መሐላ ለአንባቢው ለማብራራት የቀረበ ዳራዊ መረጃ ነው። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

እርሱ በእርግጥ መሞት ይገባዋል

እዚህ ጋ “እርሱ” የሚያመለክተው ወደ ምጽጳ ያልሄደውን ማንኛውንም ሰው ነው። ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “በእርግጥ ያንን ሰው እንገድለዋለን” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

Judges 21:6

ወንድማቸው ብንያም

ይህ የሚናገረው ስለ ብንያም ነገድ ሲሆን ለነገዱ ያላቸውን ቅርበት ለማሳየት እንደ እስራኤል ወንድም ታይቷል። አ.ት፡ “የተረፉት ብንያማውያን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)

ከእስራኤል አንድ ነገድ ተቆርጧል

የብንያም ነገድ መጥፋት ከእስራኤል በቢላዋ የተቆረጠ ያህል ተነግሯል። ይህ ግነት ነው፣ ምክንያቱም 600 ሰዎች ገና ቀርተው ነበር። ይሁን እንጂ ብንያማውያን ሴቶች ተገድለው ስለ ነበር የነገዱ የወደፊት ዕጣ ፈንታው በጥያቄ ውስጥ ነበር። አ.ት፡ “አንድ ነገድ ተደምስሷል” (ዘይቤአዊ አነጋገር፣ ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

ሴቶች ልጆቻችንን ላንድርላቸው በእግዚአብሔር ፊት መሐላ አድርገናልና ለተረፉት ለእነዚያ ሚስቶችን ማን ያመጣላቸዋል?

እስራኤላውያኑ ለተረፉት ጥቂት ብንያማውያን ሚስቶችን ለማቅረብ ፈልገዋል፣ ነገር ግን በምጽጳ ያደረጉት መሐላ ይህንን ከማድረግ አግዷቸዋል።

Judges 21:8

ኢያቢስ ገለዓድ

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

ሰዎች በኃላፊነት ስሜት ተሰብስበው ነበር

“በምጽጳ የተሰበሰቡት ሰዎች ተጠያቂነት ነበረባቸው”

ከኢያቢስ ገለዓድ ተወላጆች አንድም ሰው በዚያ አልነበረም

ይህ የሚያመለክተው ቀደም ሲል በምጽጳ የተደረገውን ጉባዔ ነው። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከኢያቢስ ገለዓድ ተወላጆች አንድም ሰው በምጽጳ አልተገኘም ነበር”

አሥራ ሁለት ሺህ

“12,000” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

የኢያቢስ ገለዓድን ተወላጆች፣ ሴቶችንና ልጆችን ጨምሮ በሰይፍ ስለት ምቷቸው

በዚህ ጥቅል መመሪያ ላይ የሚቀጥለው ቁጥር የማይመለከተው ማንን እንደሆነ ይጨምራል።

በሰይፍ ስለት ምቷቸው

“በሰይፎቻችሁ ግደሏቸው”

Judges 21:11

ኢያቢስ ገለዓድ

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 21፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ከወንድ ጋር ያልተኙ

ይህ የግብረ ሥጋ ግንኙነትን ለማመልከት በጨዋነት የተነገረ አነጋገር ነው።

አራት መቶ ወጣት ሴቶች

“400 ወጣት ሴቶች” (ቁጥሮች የሚለውን ተመልከት)

Judges 21:13

የሰላም ጥሪ አቀረቡላቸው

የነገር ስም የሆነው “ሰላም” በግሣዊ ሐረግ ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ከእነርሱ ጋር መዋጋታቸውን ለማቆም ፈለጉ” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

ኢያቢስ ገለዓድ

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። ይህንን በመሳፍንት 21፡8 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ለሁሉም የሚበቁ ሴቶች አልነበሩም

ከኢያቢስ ገለዓድ የተገኙት አራት መቶ ሴቶች ብቻ ሲሆኑ ብንያማውያኑ ስድስት መቶ ሰዎች ነበሩ።

በእስራኤል ነገዶች መካከል ልዩነትን አደረገ

“የእስራኤል ነገዶች አንድ እንዳይሆኑ አደረጋቸው”

Judges 21:16

ብንያማውያን

ይህ የሚያመለክተው የብንያምን ተወላጆች ነው። ይህንን በመሳፍንት 3፡15 ላይ እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት።

ብንያማውያን ሴቶች ተገድለው ነበርና

ይህ በአድራጊ ድምፅ ሊነገር ይችላል። አ.ት፡ “ብንያማውያን ሴቶችን በሙሉ ገደልናቸው” (አድራጊ ወይም ተደራጊ ድምፅ የሚለውን ተመልከት)

ከእስራኤል እንዳይጠፉ … ርስት መኖር አለበት

እስራኤላውያኑ እያጋነኑ ነው። ቀደም ሲል ለአራት መቶ ብንያማውያን ሚስቶችን ሰጥተዋቸዋል፣ በመሆኑም፣ ነገዱ ሙሉ በሙሉ አይጠፋም። (ግነት እና ጥቅል አስተያየት የሚለውን ተመልከት)

Judges 21:18

ለብንያም ሚስትን

እዚህ ጋ ብንያም የሚያመለክተው የብንያም ተወላጅ የሆኑትን ወንዶች ነው። አ.ት፡ “ለብንያማውያን ወንዶች ሚስት”

እርሱም ከቤቴል በስተሰሜን፣ ከቤቴል ወደ ሴኬም ከሚወስደው መንገድ በስተምስራቅና ከሊባኖስ በስተደቡብ

ይህ የሴሎ ከተማ የሚገኝበትን አካባቢ ለአንባቢው ለማብራራት የተሰጠ ዳራዊ መረጃ ነው። (ዳራዊ መረጃ የሚለውን ተመልከት)

ለቦና

ይህ የአንዲት ከተማ ስም ነው። (ስሞች እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚለውን ተመልከት)

Judges 21:20

እያንዳንዳችሁ ሚስት የምትሆናችሁን ጥለፉ … ተመልሳችሁ ወደ ብንያም ምድር ሂዱ

ብንያማውያኑ እነዚህን ሴቶች ይዘው ወደ ገዛ ምድራቸው ተመልሰው እንደሚሄዱ ይታወቃል። የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “እያንዳንዳችሁ ከሴሎ ልጃገረዶች አንዷን መያዝና ሚስት እንድትሆናችሁ ከእናንተ ጋር ወደ ብንያም ምድር መውሰድ ይኖርባችኋል”

Judges 21:22

ምህረት አሳዩን

የነገር ስም የሆነው “ምህረት” እንደ ድርጊት ሊተረጎም ይችላል። አ.ት፡ “ደግነትን አድርጉልን” (የነገር ስም የሚለውን ተመልከት)

በጦርነቱ ጊዜ ለእያንዳንዱ ወንድ ሚስት ስላላገኘንለት ነው

የዚህ መግለጫ ሙሉ ትርጉም ግልጽ መደረግ ይችላል። አ.ት፡ “ከኢያቢስ ገለዓድ ጋር በተዋጋን ጊዜ ለእያንዳንዳቸው ሚስት ስላላገኘን”

ሴት ልጆቻችሁን ለእነርሱ ላለመስጠት … ንጹሐን ናችሁ

ይህ የሚያመለክተው የሴሎን ሰዎች ነው። እነርሱ ሴቶች ልጆቻቸውን ለብንያማውያን በፈቃደኝነት አልሰጡም፣ በመሆኑም ይህንን ላለማድረግ የገቡትን መሐላ አላፈረሱም።

Judges 21:23

የሚያስፈልጓቸው ሚስቶች ቁጥር

ይህ የሚያመለክተው ከኢያቢስ ገለዓድ ሚስቶችን ላላገኙ ሁለት መቶ ብንያማውያን ለእያንዳንዳቸው አንዲት ሚስት ነው። (መሳፍንት 21፡14ን ተመልከት)።

Judges 21:25

በእስራኤል ንጉሥ አልነበረም

“እስራኤል ገና ንጉሥ አልነበራትም”

በዐይኑ ፊት ትክክል የመሰለውን

ዐይን ማየትን፣ ማየትም አሳብን ወይም ፍርድን ይወክላል። አ.ት፡ “ልክ ነው ብሎ የሚፈርደውን” ወይም “ልክ ነው ብሎ የሚያስበውን” (ዘይቤአዊ አነጋገር የሚለውን ተመልከት)


Book: Ruth


Ruth

Chapter 1

1 መሳፍንት ይገዙ በነበረበት ዘመን በምድሪቱ ላይ ራብ ነበረ። አንድ ከበተልሔም ይሁዳ የሆነ ሰው ከሚስቱና ከሁለቱ ልጆቹ ጋር ወደ ሞአብ አገር ሄደ፡፡ 2 የሰውዮው ስም አቤሜሌክ ይባል ነበር፣ የሚስቱም ስም ኑኃሚን ይባላል፡፡ የሁለቱም ወንዶች ልጆቹ ስም መሐሎንና ኬሌዎን፣ የይሁዳ ቤተልሔም ኤፍራታውያን ነበሩ፡፡ እነርሱም ወደ ሞዓብም አገር ደረሱና በዚያ ተቀመጡ፡፡ 3 የኑኃሚንም ባል አቤሜሌክ ሞተ እርስዋም ከሁለቱ ወንዶች ልጆችዋ ጋር ቀረች፡፡ 4 እነዚህ ወንዶች ልጆች ከሞዓባውያን ሴቶች ሚስቶችን ወሰዱ፤ የአንዷ ስም ዖርፋ ነበር፣ የሌላኛዋ ስም ደግሞ ሩት ነበረ። በዚያም ለአሥር ዓመታት ያህል ተቀመጡ፡፡ 5 ከዚያም መሐሎንና ኬሌዎን ሁለቱም ሞቱ፣ ኑኃሚንም ያለ ባልዋና ያለ ሁለቱ ልጆችዋ ብቻዋን ተለይታ ቀረች፡፡ 6 በዚያን ጊዜ ኑኃሚን ከሁለቱ ምራቶችዋ ጋር ሞአብን ለመልቀቅና ወደ ይሁዳ ለመመለስ ወሰነች፡፡ እርስዋም በሞዓብ ምድር ሳለች እግዚአብሔር የተቸገሩትን ሕዝቡን እንደረዳቸውና መብልን እንደ ሰጣቸው ሰማች፡፡ 7 ስለዚህ እርስዋ ከሁለቱ ምራቶችዋ ጋር ከነበረችበት ስፍራ ለቀቀች፣ ከዚያም ወደ ይሁዳ ምድር ለመመለስ መንገዱን ይዘው ወደታች ሄዱ፡፡ 8 ኑኃሚን ለምራቶችዋ “ሂዱ፣ እያንዳንዳችሁ ወደ እናታችሁ ቤት ተመለሱ፡፡ ለሞቱትና ለእኔ ታማኝነት እንዳሳያችሁን ሁሉ፣ እግዚአብሔር ለእናንተ ታማኝነቱን ያሳያችሁ፡፡ 9 ጌታ እያንዳንዳችሁን በሌላ ባል ቤት ዕረፍት ይስጣችሁ” አለቻቸው፡፡ ከዚያም ሳመቻቸው፣ እነርሱም ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ፡፡ 10 እነርሱም “አይሆንም! ከአንቺ ጋር ወደ ሕዝብሽ እንመለሳለን” አሉአት፡፡ 11 ኑኃሚን ግን “ልጆቼ ሆይ፣ ተመለሱ! ለምን ከእኔ ጋር ትሄዳላችሁ? ባሎቻችሁ ይሆኑ ዘንድ ለእናንተ የሚሆኑ ወንዶች ልጆች በማሕጸኔ አሁን አሉን? 12 ልጆቼ ሆይ፣ ተመለሱ፣ በራሳችሁ መንገድ ሂዱ፤ ባል ለማግባት በጣም አርጅቻለሁና፡፡ ዛሬ ማታ ባል አገኛለሁ ብየ እንኳ ተስፋ ባደርግና ወንዶች ልጆችን ብወልድ፣ 13 እነርሱ እስኪያድጉ ድረስ ትጠብቃላችሁን? እየጠበቃችሁ አሁን ባል ሳታገቡ ትቀራላችሁን? አይሆንም፣ ልጆቼ ሆይ! ከእናንተ ይልቅ ሁኔታው እኔን እጅግ በጣም ያስመርረኛል፣ ምክንያቱም የእግዚአብሔር እጅ በእኔ ላይ ወጥቶአልና፡፡ 14 በዚያን ጊዜ ምራቶችዋ ድምፃቸውንም ከፍ አደረጉና እንደገና አለቀሱ፡፡ ዖርፋም አማትዋን ሳመቻትና ተሰናበተቻት፣ ሩት ግን ተጠግታ ያዘቻት፡፡ 15 ኑኃሚንም “አድምጪኝ፣ እነሆ የባልሽ ወንድም ሚስት ወደ ሕዝብዋና ወደ አማልክትዋ ተመልሳለች፡፡ ከባልሽ ወንድም ሚስት ጋር አንቺም ተመለሽ” አለቻት፡፡ 16 ነገር ግን ሩት “ከአንቺ ርቄ እንድሄድ አታድርጊኝ፣ ወደምትሄጅበት እሄዳለሁና፤ በምትቆይበትም እቆያለሁና፤ ሕዝብሽ ሕዝቤ ይሆናል፣ አምላክሽም አምላኬ ይሆናል፡፡ 17 በምትሞችበትም እሞታለሁ፣ በዚያም እቀበራለሁ፡፡ ከሞት በቀር እኛን አንድም ነገር ቢለየን እግዚአብሔር ይቅጣኝ፣ ከዚህም በላይ ያድርግብኝ” አለቻት፡፡ 18 ኑኃሚን ሩት ከእርስዋ ጋር ለመሄድ እንደ ወሰነች ባየች ጊዜ፣ ከእርስዋ ጋር መከራከር አቆመች፡፡ 19 ስለዚህ ሁለቱም ወደ ቤተ ልሔም ከተማ እስኪመጡ ድረስ ተጓዙ፡፡ ወደ ቤተ ልሔምም በደረሱ ጊዜ፣ ከተማው በሙሉ ስለ እነርሱ እጅግ በጣም ተደነቁ፡፡ ሴቶችም “ይህች ኑኃሚን ናትን?” አሉ፡፡ 20 እርስዋ ግን “ኑኃሚን ብላችሁ አትጥሩኝ፡፡ ሁሉን የሚችል አምላክ ሕይወቴን መራራ አድርጎታልና፣ ማራ በሉኝ” አለቻቸው፡፡ 21 በሙላት ሄድሁ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ወደ ቤቴ ባዶዬን እንደገና መለሰኝ፡፡ ታዲያ እግዚአብሔር አዋርዶኝ፣ ሁሉንም የሚችል አምላክ አስጨንቆኝ እያያችሁ ለምን ኑኃሚን ትሉኛላችሁ?” አለቻቸው፡፡ 22 ስለዚህ ኑኃሚንና ምራትዋ ሞአባዊት ሩት ከሞዓብ አገር ተመለሱ፡፡ እነርሱ የገብስ መከር በተጀመረ ጊዜ ወደ ቤተልሔም መጡ፡፡



Ruth 1:1

እንዲህም ሆነ

“እንዲህም ሆነ” ይሄ የተለመደ የታሪካዊ ተረካ አጀማመር ነው።

መሳፍንት በሚገዙበት ዘመን

“መሳፍንት ይፈርዱ በነበረ ገዜ”

በምድሪቱ

ይሄ የሚያመላክተው የእስራኤልን ምድር ነው። “በአገሩ”

አንድ ሰውም

“አንድ ሰው” ይሄ አንድን ገፀባህሪ ወደ ትረካው ማስገቢያ (ማስተዋወቅያ)ተልምዷዊ መንገድ ነው።

የቤተልሔም ይሁዳ የኤፍራታ ሰዎች

ከኤፍሬም ጎሳ(ነገድ)የሆኑ፤ በይሁዳ ክልል በሆነው በቤተልሄም የሰፈሩ ሰዎች ነበሩ።

Ruth 1:3

እርሷ እና ሁለቱ ልጆችዋ በቻ ቀሩ

“ኑኃሚንም ከሁለት ልጆቿ ጋር በቻዋን ቀረች“

ሚስት አገቡ (ወሰዱ)

”ሴቶች ሚስት አገቡ (ወሰዱ)“ ይሄ ሚስት ማግባትን ያመላክታል

ከሞዓባውያን ሴቶች

የኑኃሚን ወንድ ልጆች ከሞዓብ ጎሳ (ነገድ)የሆኑ ሴቶች። ሞዓባውያን ሌሎች አማልክትን ያመልኩ ነበር።

የአንዲቱ ስም . . . የሁለተኛይቱም ስም

“. . . የተባሉ የሞዓብ ሴቶች“

አስር ዓመት ያህል

አቤሜሌክ እና ኑኃሚን ወደ ሞዓብ ከመጡ ከአስር ዓመት በኋላ፤ ልጆቻቸው መሓሎን እና ኬሌዎን ሞቱ።

ተለይታ ቀረች

ኑኋሚን መበለት ሆነች።

Ruth 1:6

ርሷም በሞአብ ምድር ሳለች

“እርሷም በሞአብ ሳለች”። ዜናው የመጣው ከእስራኤል አገር እንደሆነ ያመላክታል። እግዚአብሄር እስራኤልን እንደጎበኘ በሞአብ ምድር ሳለች ሰማች።

እግዚአብሔር

በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለህዝቡ የተገለጠበት ስም ነው። (የእግዛብሔርን ስም ስለመተርጎም በቃላት አተረጓጎም መምሪያ ገፁ ላይ ተመልከቱ)

ሕዝቡን እንደጎበኘ እና እህል እንደሰጣቸው

ሕዝቡን እንደጎበኘ እንጀራም እንደሰጣቸው

ምራቶቿን

ምራቶችዋ፤ ወንድ ልጆቿን ያገቡት ሴቶች

መንገድ ይዘው ጉዟቸውን ቀጠሉ

“የሚመልሳቸውን መንገድ ይዘው።” መንገድ ይዘው የሚለው በአንድ መንገድ መሄድን የሚያመላክት አባባል ነው።

Ruth 1:8

ምራቶች

የወንድ ልጆች ሚስቶች ወይንም የወንድ ልጆቿ መበለቶች

እያንዳንዳችሁ

ኑኃሚን የምታዋራው ሁለት ሰዎችን ነበር፤ ከዚህ በመቀጠልም እናንተ ብላ ስትናገር ሁለቱን በማስመልከት ነው።

ወደ እናቶቻችሁ ቤት

“ወደ እናቶቻችሁ ቤትም”

በጎ ነገር እንዳደረጋችሁ

“ቸርነትን እንዳደረጋችሁ”

በጎነት

“ቸርነት” የ ፍቅር፣ የበጎነት፣ እና ታማኝነትን ያመላክታል።

ለሞቱት

“ለሞቱት ባሎቻችሁ” ን ኡኃሚን በዚህ የሞቱትን ልጆችዋን ማመላከት ነው የፈለገችው።

ያድርግላችሁ

“እንደዚሁ ያድርግላችሁ” ወይንም “እንዲደረግላችሁ ይፍቀድ”

ያሳሪፋችሁ

እዚህ ጋር “ያሳርፋችሁ” የሚለው በትዳርም የሚገኘውን ደህንነትን ያጠቃልላል።

በምታገቡት ባል ቤት

ከአዳዲስ ባሎቻችሁ፣ ከሌላ ሰው ባል ጋር አይደለም። ይሄ የሚያመላክተው በባልየው ቤት ውስጥ እና ከባልየው የሃፍረት ከለላ ስር ማለት ነው።

እነርሱም ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ

ድምፅን ከፍ ማድረግ ለጮክ በሎ ማውራትን የሚያመላክት አባባል ነው። ምራቶቷም ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ወይንም አምርረው አለቀሱ።

ተመልሰን … እንሄዳለን

“እንመለሳለን” ዓርፋ እና ሩት “እኛ” ብለው ሲናገሩ ስለራሳቸው እንጂ ስለ ሩት አንነበረም የሚናገሩት።

ከአንቺ ጋር

እዚህ ጋር “አንቺ” የሚለው የሚያመላክተው ኑኃሚንን ነው።

Ruth 1:11

ከእኔ ጋር ለምን ትሄዳላችሁ?

ይህ ምላሽ የሚሰጥለት ጥያቄ አይነት አይደለም። “ከእኔ ጋር መሄዱ ትርጉም አይሰጥም።” ወይንም “ከእኔ ጋር መሄድ የለባችሁም።”

ባል የሚሆኗችሁ ሌሎች ልጆች ከእንግዲህ የምወልድ ይመስላችኋልን?

ኑኃሚን በዚህ ጥያቄዋ ለእነርሱ የሚሆኑ ወንድ ልጆች ከዚህ ወድያ ልትወልድላቸው እንደማትችል ትናገራለች። “መቼስ ለእናንተ ባል መሆን የሚችሉ ሌሎች ወንድ ልጆች ከዚህ በኋላ መውለድ አልችልም።”

ባል እንዳላገባ እጅግ አርጅቻለሁ

ባል የማግባቱ ምክንያት በግልፅ ተጠቅሷል። “ሌሎች ወንድ ልጆች እንዳልወልድ”

ልጆች ብወልድ

“መፀነስ” ወይንም “ወንድ ልጆች መውለድ”

እስኪያድጉ ድረስ ትጠብቃላችሁን? እነርሱን በመጠበቅ እስከዚያ ሳታገቡ ትቈያላችሁን?

እነኚህ ምላሽ የሚሰጥላቸው ጥያቄዎች አይነት አይደሉም። “ታገብዋቸው ዘንድ እስኪያድጉ አትጠብቋቸውም። አሁን ማግባትን ትመርጣላችሁ”

ሁኔታው ከእናንተ ይልቅ ለእኔ እጅግ መራራ ነው

መራራነት የሃዘን እና የሰቆቃ መገለጫ ነው፤ በዚህም የሃዘንዋ መንሳኤ ምን እንደሆነ ማወቁ አያዳግትም። “የእናንተ ባል አለመኖር እኔን ያሳዝነኛል።

የእግዚአብሔር እጅ በእኔ ላይ ተነሥቶአልና

“እጅ” የሚለው የእግዚአበሔርን ኃይል ወይንም ተፃዕኖ ያሳያል። “የእግዚአብሔር እጅ በእኔ ወጥቶአልና።”

Ruth 1:14

ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ

ይህ የሚያመላክተው አምርረው እንዳለቀሱ እና ጮክ ብለው እንደተጣሩ ነው።

እነሆ የባልሽ ወንድም ሚስት

“ልብ በይ፤ ምክኛቱም አሁን የምልሽ ነገር እውነትና ጠቃሚ ነው፤ ባልንጀራሽ።”

ሩት ግን ልትለያት ስላልፈለገች ተጠመጠመችባት

“ሩት ኝ ተጠጋቻት።” “ሩት ልትለያት አልወደደችም።” ወይንም “ ሩት አልለያትም አለች።”

የባልሽ ወንድም ሚስት

“ባልንጀራሽ”

አማልክትዋ

ዓርፋ እና ሩት ልጆችዋን ከማግባትዋ በፊት የሞአባውያንን አማልክት ያመልኩ ነበር። በትዳራቸዋም ውስጥ ሳሉ የኑኃሚንን አምላክ ማምለክ ጀምረው ነበር።

Ruth 1:16

ወደ ምትሄጅበት

“ወደ ምትኖሪበት”

ሕዝብሽ ሕዝቤ

ሩት በዚህ የምታመላክተው የኑኃሚንን ህዝቦች ነው፤ እስራኤላውያንን። “የአገርሽን ሕዝቦች እንደ እራሴ ሕዝቦች እቆጥራለሁ።” ወይንም “ዘመዶችሽን እንደ ዘመዶቼ እቆጥራለሁ።”

በምትሞቺበት እሞታለሁ

ይህ ሩት እስከ ዕድሜዋ ፍፃሜ ከኑኃሚን ጋር በአንድ ቦታ እና ከተማ የመሆን ፍላጎቷን ያሳያል።

ብለይሽ እግዚአብሔር ይፍረድብኝ፤ ከዚህም የከፋ ያድርግብኝ።

ይህ የሚያመላክተው ሩት አደርጋለሁ ያለችውን ባታደርግ፤ እግዚአብሔር እንዲቀጣት እየጠየቀች እንደሆነ ነው። “እግዚአብሔር አይፍቀድ እንደማለት ነው።”

ከመናገር ዝም አለች

“ኑኃሚን ሩትን መጐትጐቷን ተወች”

Ruth 1:19

እንደ ደረሱም

“እንዲህ ሆነ።” ይህ የታሪኩ አዲስ ምዕራፍ መነሻ አመላካች ነው።

ከተማው በሙሉ

“ከተማው” የሚለው በዛ የሚኖሩ ሰዎችን በሙሉ ያመላክታል። “የከተማይቱ ሰዎች ሁሉ።”

ይህች ኑኃሚን ናትን?

ኑኃሚን በቤተልሔም ከኖረች በዙ ዓመታትን አስቆጥሯል በሎም ባሏ እና ወንድ ልጆቿ አብረዋ አልነበሩም፤ እናም በዛ የነበሩት ሴቶች ኑኃሚን ስለመሆኗ መጠራጠራቸውን የሚያመናክት እባባል ነው። እንደ እውነተኛ ጥያቄ ቁጠሩት።

ኑኃሚን ብላችሁ አትጥሩኝ

“ኑኃሚን” የሚለው ስም “የእኔ ደስታ” የሚል ትርጉም ነው ያለው። ኑኃሚንም ባሏን እና ልጆቿን ስላጣች፤ ስሟ ሕይወቷን እንደሚመጥን አይሰማትም።

ማራ

መራራ፤ የስሙ ትርጉም ሲሆን፤ ብዙውን ግዜ ይህ ስም ሲተረጎም እንደሚያወጣው ስም “ማራ” ተበሎ ይተረጎማል።

በሙላት ወጣሁ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ባዶዬን መለሰኝ

ኑኃሚን ከቤተልሔም ስትወጣ በልዋ እና ሁለት ወንዶች ልጆችዋ በሕይወት ነበሩ፤ ደስተኛም ነበረጭ ኑኃሚን ለባልዋ እና ሁለት ልጆችዋ ሞት ተጠያቂ የምታደርገው እግዚአብሔርን ነው። ወደ እስራኤልም ብቻዋን እንድትመለስ ያደረገው እርሱ ነው።

አስጨንቆኛል

“ፍርድን አሳልፎብኛል።”

አዋርዶኛል

መከራ አምጥቶብኛል

Ruth 1:22

ኑኃሚንም እና . . . ሩት

“ኑኃሚንም” የሚለው ቃል መደምደምያ የሆነውን መጨረሻ ላይ የሆነውን ነገር ጠቋሚ አያያዥ ቃል ያሳያል። በእናንተ ቋንቋ ይህንን ሊተካ የሚችን ቃል ተጠቀሙ።

የገብስም መኧር በደረሰ ግዜ

“የገብስ አዝመራ” የሚለውን ስንኝ ሊተካ በሚችል ቅል ሊተረጎም ይችላል። “የገብስ አዝመራ በሚሰበሰብበት ወቅት”


Chapter 2

1 የኑኃሚን ባል አቤሜሌክ፣ በጣም ባለጠጋና ኃያል ሰው የሆነ ቦዔዝ የሚባል ዘመድ ነበረው፡፡ 2 ሞዓባዊቱ ሩት ኑኃሚንን “አሁን ልሂድና ወደ እርሻዎች ገብቼ እህል ልቃርም፡፡ በፊቱ ሞገስ የማገኘውን ሰው እከተላለሁ” አለቻት፡፡ ኑኃሚንም “ልጄ ሆይ፣ ሂጂ” አለቻት፡፡ 3 ሩት ሄደችና ከአጫጆችም በኋላ በእርሻ ውስጥ ቃረመች፡፡ እርስዋም የአቤሜሌክ ዘመድ ወደሆነው ወደ ቦዔዝ እርሻ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ደረሰች። 4 እነሆም፣ ቦዔዝ ከቤተ ልሔም መጣና ለአጫጆቹ “እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን” አላቸው፡፡ እነርሱም “እግዚአብሔር ይባርክህ” ብለው መለሱለት፡፡ 5 ከዚያም ቦዔዝ በአጫጆቹ ላይ ተቆጣጣሪ የነበረውን አገልጋዩን “ይህች ወጣት ሴት የማን ናት?” አለው፡፡ 6 አጫጆቹንም የሚቆጣጠረው አገልጋይ “ይህች ወጣት ሞዓባዊት ከሞዓብ ምድር ከኑኃሚን ጋር የመጣች ናት” አለው፡፡ 7 እርስዋም ‘ከአጫጆቹ በኋላ እየተከተልሁ የእህል ቃርሚያ እንድቃርምና እንድለቅም እባክህ ፍቀድልኝ አለች’ አለው፡፡ ስለዚህ እርስዋም ወደዚህ መጣች፣ በቤት ጥቂት ከማረፍዋ በስተቀር፣ ከጠዋት ጀምራ እስከ አሁን ድረስ መቃረም ቀጥላለች፡፡” 8 የዚያን ጊዜ ቦዔዝ ሩትን “ልጄ ሆይ፣ እኔን እያዳመጥሽኝ ነውን? ወደ ሌላ እርሻ ሄደሽ አትቃርሚ፤ ከእርሻየ አትሂጂ፣ ይልቁንም በዚህ ቆዪና ከወጠት ሴቶች ሰራተኞቼ ጋር አብረሽ ስሪ፡፡ 9 ዓይኖችሽ ሰዎቹ ወደሚያጭዱበት ስፍራ ብቻ ይመልከቱ፣ ሌሎቹንም ሴቶች ተከተያቸው፡፡ ሰዎቹን እንዳይነኩሽ አላዘዝኋቸውምን? ሲጠማሽ ወደ ውኃ ማሰሮዎቹ ሄደሽ ወንዶቹ ከቀዱት ውኃ መጠጣት ትችያለሽ” አላት፡፡ 10 ከዚያም በግንባርዋ መሬቱን በመንካት በቦዔዝ ፊት ሰገደች፡፡ እርስዋም “እኔ እንግዳ የሆንሁት ታስበኝ ዘንድ በአንተ ፊት ሞገስ ያገኘሁት ለምንድን ነው?” አለችው፡፡ 11 ቦዔዝም ለእርስዋ “ባልሽ ከሞተበት ጊዜ ጀምሮ የሰራሽው ስራ ሁሉ ለእኔ ተነግሮኛል፡፡ አማትሽን ለመከተልና ወደ ማታውቂው ሕዝብ ለመምጣት አባትሽንና እናትሽን የተወለድሽባትንም ምድር ትተሻል፡፡ 12 ስለ ስራሽ እግዚአብሔር ይክፈልሽ፡፡ ከክንፉ በታች መጠጊያ ካገኘሽበት ከእስራኤል አምላክ ከእግዚአብሔር ሙሉ ደመወዝሽን ተቀበይ” አላት፡፡ 13 እርስዋም “ጌታዬ ሆይ፣ ምንም እንኳ እኔ ከሴት አገልጋዮችህ እንደ አንዲቱ ባልሆንም አጽናንተኸኛልና፣ እኔን በደግነት አናግረኸኛልና በፊትህ ሞገስን ላግኝ” አለቸው፡፡ 14 በምሳም ጊዜ ቦዔዝ ለሩት እንዲህ አላት፡- “ወደዚህ ነይ፣ እንጀራም ብዪ፣ ጉርሻሽንም በሆምጣጤው ወይን አጥቅሺው፡፡” በአጫጆቹም አጠገብ ተቀመጠች፣ እርሱም የተጠበሰ እህል ሰጣት፣ እርስዋም እስክትጠግብ ድረስ በላች፣ የቀረውንም አተረፈች፡፡ 15 ለመቃረም ስትነሳ፣ ቦዔዝ ወጣት አገልጋዮቹን “በነዶው መካከልም እንድትቃርም ፍቀዱላት፣ ምንም መጥፎ ነገር ለእርስዋ አትናገሩአት፡፡ 16 ደግሞም ከነዶው ዘለላዎች አስቀርታችሁ በእርግጠኝነት ልተተዉላት ይገባል፣ እንድትቃርም ለእርስዋ ተዉላት፡፡ እርስዋንም አትውቀሱአት” ብሎ አዘዛቸው፡፡ 17 ስለዚህ በእርሻው ውስጥ እስከ ማታ ድረስ ቃረመች፡፡ ከዚያም የቃረመችውን እህል ወቃችው፣ የወቃችውም እህል አንድ የኢፍ መስፈሪያ ያህል ገብስ ሆነ፡፡ 18 እርስዋም ተሸክማው ወደ ከተማ ሄደች፡፡ አማትዋም የቃረመችውን አየች፡፡ ሩትም በልታ ከጠገበች በኋላ የተረፋትን የተጠበሰ እህል አውጥታ ለእርስዋ ሰጠቻት፡፡ 19 አማትዋም ለእርስዋ እንዲህ አለቻት፡-“ዛሬ የቃረምሽው ወዴት ነው? ለመስራትስ ወዴት ሄድሽ? የረዳሽ ሰው የተባረከ ይሁን፡፡” ከዚያም ሩት ለአማትዋ የቃረመችበት እርሻ ባለቤት ስለሆነው ሰው ነገረቻት፡፡ እርስዋም “ዛሬ ቃርሚያ የቃረምሁበት እርሻ ባለቤት ስሙ ቦዔዝ ይባላል” አለቻት፡፡ 20 ኑኃሚንም ለምራትዋ “ታማኝነቱን በሕያዋንና በሙታን ላይ ባልተወው በእግዚአብሔር የተባረከ ይሁን” አለቻት፡፡ ኑኃሚንም ደግሞ “ይህ ሰው ለእኛ የቅርብ ዘመዳችን ነው፣ ከሚቤዡን አንዱ ነው” አለቻት፡፡ 21 ሞዓባዊቱ ሩትም “በእርግጥም፣ እንዲህ አለኝ፣ ‘መከሬን ሁሉ እስኪጨርሱ ድረስ ከወጣት ወንዶች ሰራተኞቼ አትራቂ፡፡’” 22 ኑኃሚንም ለምራትዋ ለሩት “ልጄ ሆይ፣ ከወጣት ሴቶች ሰራተኞቹ ጋር ብትወጪ መልካም ነው፣ በሌላ በየትኛውም እርሻ ጉዳት እንዳያገኝሽ” አለቻት፡፡ 23 ስለዚህም እርስዋ እስከ ገብሱና ስንዴው መከር መጨረሻ ድረስ ልትቃርም ወደ ቦዔዝ ሴቶች ሰራተኞች ተጠግታ ቆየች፡፡ እርስዋም ከአማትዋ ጋር ትኖር ነበር፡፡



Ruth 2:1

ለኑኃሚን ባል የሚዛመደው

ይህ ስንኝ ትረካው ከመቀጠሉ በፊት አዲስ መረጃን ያስተዋውቃል። በእናንተ ቋንቋ አዲስ መረጃን ወደ ምንባብ ለማስተዋወቅ የምትጠቀሙበት መንገድ ካለ እርሱን ተጠቀሙ።

ኃያል ሰው

“ባለጸጋ” ይህ የሚያሳየው ቦኤዝ ባለጸጋ እና በማህበረሰቡ በመልካም ዝና የታወቀ ሰው ነበረ።

ማዓባዊቷ ሩትም

እዚህ ጋር ትረካው ይቀጥላል። በቋንቋችሁም ታሪክ ከተቋረጠ በኋላ እንዴት እንደሚቀጥል ልብ በሉ።

ማዓባዊቷ

ሴቲቱ ከሞዓብ ስለመሆኗ መጠቆምያ ሌላኛው መንገድ ነው።

ቅርሚያ የሚያስቃርም

“ከእህሉ ዘለላ እንድቃርም” ወይንም “አጨዳ ላይ ከኋላ የተተወ የእህል ዘለላ ለማንሳት”

የእህል ዘለላ

“ዕራሱ” ወይንም “ክምችቱ” የእህሉን ዋና ፍሬ የያዘ “ዘለላ”።

በፊቱ ሞገስ የማገኘውን

“በፊቱ ሞገስ ማግኘት” የሚለው አባባል በሰው ዘንድ ተቀባይነት ማግኘትን ያመላክታል። ሩት ፈቃድ ማግኘትን በአንድ ሰው ፊት ሞገስን እንደማግኘት አድርጋ ትናገራለች። በፊቱ፤ የሚለው አገላለፅ በመታየት፣ በአስተሳሰብ እና በአወሳሰን ተቀባይነት ማግኘትን ያመላክታል።

ልጄ

ሩት ኑኃሚንን እንደ እናቷ ነበር የምትንከባከባት። ብትርጉም ቋንቋው ልጅን የሚተካ ቃል መጠቀም ከተቻለ እርሱን መጠቀም ይቻላል።

Ruth 2:3

እንደአጋጣሚም

ሩት ስትቃርምበት የነበረው እርሻ የኑኃሚን ዘመድ የሁነው ቦኤዝ እርሻ መሆኑን አታውቅም ነበር።

እነሆም፥ ቦኤዝ

“እነሆም” የሚለው ቃል የቦኤዝ መምጣት በታሪኩ ላይ የሚጫወተውን ትልቅ ሚና አመላካች ነው። የዚህ ዓይነት ሚና የሚጫወት ቃል በቋንቋችሁ ካለ እርሱን መጠቀም አስፈላጊ ነው።

ከቤተልሔም መጣ

እርሻው ከቤተልሔም ያልታወቀ ዕርቀት ላይ ይገኛል።

ይባርክህ

“መልካምን ነገር ይስጥህ” ወይንም “ደስተኛ ያርግህ”

Ruth 2:5

ይህች ወጣት ሴት የማን ናት?

ቦኤዝ እዚህ ጋር እየጠየቀ ያለው 1) ስለ ሩት ባል ወይንም 2) ስለሩት ወላጆች ውይንም ጠባቂዎች ነው።

አዛዥ

“ኃላፊነት ላይ ያለው” ወይንም “እየተቆጣጠረ ያለው”

በቤት

“በጎጆ” ወይንም “በመጠለያ” ይሄ በእርሻ መሃከል ከፀሃይ ጊዜያዊ መጠለያ ወይንም የመናፈሻ ጎጆ ነበር።

Ruth 2:8

ልጄ ሆይ፥ ትሰምያለሽ

የሄ እንደ ትዕዛዝ ቃል ልንመለከተው እንችላለን። “ስሚኝ ልጄ” ወይንም የምለውን ነገር ልብ በይ ልጄ።”

ልጄ

ይሄ በዕድሜ የሚያንስ ሰወን የመናገርያ መንገድ ነው። ሩት የቦኤዝ ልጅ አይደለችም። ይህ ቃል ሲተረጎም ልጅን ለማለት ተፈልጎ አለመሆኑን ልብ የበሉ።

ወደምያጭዱበት ስፍራ ተመልከቺ

መመልከት አንደን ነገር ማየትን እና አትክሁሮት መስጠትን ያመለክታል። “እርሻውን ብቻ ተመልከቺ” ወይንም “ለእርሻው ብቻ አትክሁሮት ስጪ።”

አዝዣለሁ

“አላዘዝኩምን?” የሚል ጥያቄ አዘል፤ ንግግሩ ማስረገጫ ቃል። “ጉበዛዚቱን አዝዣለሁ።”

ወንዶቹ . . . ልጃገረዶቹ

“ወጣት ወንድ ሰራተኞች . . . ወጣት ሴት ሰራተኞች።” ወንዶሽ የሚለው ቃል በተደጋጋሚ ጥቅም ላይ ይውላል። ወይንም ጎበዛዚቱ ይለዋል፤ ይሄ በእርሻው ላይ በአጨዳ ላይ ያሉ ሰራተኞችን ያመላክታል።

እንዳያስቸግሩሽ

ለማለት የተፈለገው፤ 1) ወንዶቹ እንዳይጎዱሽ። 2) በዚህ እርሻ ከመቃረም እንዳይከለክሉሽ።

ጎበዛዚቱ ከቀዱት ወሃ

ከቀዱት ማለት ከውሃ ገድጓድ ካወጡት ወይንም ውሃ ከማጠራቀምያው ማድጋ ካወጡጥ

Ruth 2:10

በግንባርዋም ተደፍታ፥ በምድር ላይ ሰገደችለት

ይሄ የአክብሮት የፍርሃት ማሳያ ነው። ስላደረገላት ነገር በማመስገን ለቦኤዝ አክብሮትን እያሳየች ነው። የትህትናም ማሳያ ነው።

ባይተዋር የሆንኩት እኔ . . . በፊትህ ሞገዝ ለማግኘት የበቃሁት እንዴት ነው?

ሩት ከልብዋ ትክክለኛ ጥያቂአን እየጠየቀች ነው።

ባይተዋር

ሩት በግልዋ ለእስራኤል አምላክ ተሰጥታለች፤ ነገር ግን በውጪው የምትታወቀው እንደ “ሞዓባዊቷ” ነው።

ነግረውኛል

“ሰምቻለሁ” ይሄ በቀጥተኛ መልኩ፤ “ሰዎች ነግረውኛል” ተብሎ ሊተረጎም ይችላል።

ሕዝብ እንደመጣሽ

ቦኤዝ መጠቆም የፈለገው ሩት በማታውቀው የኑኃሚን መንደር፣ አገር እና ኃይማኖት መሃከል ለመኖር መምጣቷን ነው።

ዋጋሽን ይክፈልሽ

“ይስጥሽ” ወይንም “መልሶ ይክፈልሽ”

ስላደረግሽው

“ለሰራሽ” ለታማኝነትሽ፤ ከኑኃሚን ጋር በቤተልሄም ለመኖር ስለመምረጥሽ እና የኑኃሚንን አምላክ ስላመንሽ።

በእግዚአብሔር ዘንድ ደሞዝሽ ፍጹም ይሁን

ይሄ ቅኔአዊ አገላለፅ ሲሆን፤ ከዚህ በፊት ካለው ዓረፍተ ነገር ጋር ይመሳሰላል። “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ብድራትሽን አትረፍርፎ ይመልስልሽ”

በክንፉ ጠላ ሥር ለመጠለል የመጣሽበት

ቦኤዝ እግዚአብሔር የሚተማመኑበትን እንዴት አድርጎ እንደሚከልል ለመግለፅ የሚጠቀመው ንፅፅር፤ ወፎች ጫጩቶቿን በክንፏ ጥላ ስር የምታደርግላቸውን እንክብካቤ ነው። “

Ruth 2:13

በዓይንህ ሞገስ ላግኝ

“ሞገስ ላግኝ” የሚለው ተቀባይነት ማግኘትን ወይንም በእርስዋ ደስተኛ መሆንን ያመላክታል። “በዓይኖችህ” የሚለው ምልከታን የሚያሳይ ሲሆን፤ ምልከታም የእርሱን ግምገማ ለማሳየት የሚጠቅም ዘይቤአዊ አገላለፅ ነው።

ከባርያዎቹ እንደ አንዲቱ ሳልሆን

ይህ ቃል ሊኖረው የሚችለው ትርጉም 1) ሩት ከቦኤዝ አገልጋዮች መሃከል አንዷ አልነበረችም። 2) ሩት ከ ኑኃሚን ልጆች መሃከል አንዱን ማግባቷ በቤተልሔም ምንም ዓይነት ጥቅም እንደምያስገኝላት አላሰበችም።

Ruth 2:14

በምሳም ግዜ

ይህ የሚያሳየው በዕኩለ ቀን መሆኑን ነው።

እንጀራሽንም በሆምጣጤው አጥቅሽ

ይህ በዕርሻ የሚበላ ቀላል ምግብ ነው። ሰዎች መሬት ላይ የተነጠፈ ምንጣፍ ላይ ይቀመጣሉ፤ በመሓከልም የወይን ሆምጣጥጤ ይቀመጥና በተቆረሰ እንጀራ እያጠቀሱም ይመገባሉ።

የወርይ ሆምጣጤ

በእንጀራ እየተጠቀሰ የሚበላ። እስራኤላውያን ይህንን ወይን ይበልጥ ሆምጣጤ እንዲሆን ያፈሉት ነበር።

Ruth 2:15

ደግሞም ልትቃርም በተነሳች ግዜ፤ ቦኤዝ ጎበዛዝቱን

በዚህ ትዕዛዝ ዐውድ ውስጥ፣ ቦኤዝ ይህንን መመርያ ሲሰጥ ሩት ልጸማ በማትችልበት ዕርቀት ላይ እንደነበረ እንረዳለን።

ስትነሳም

“ስትቆምም”

በነዶው መካከል እንኳ

“እንኳ” የሚለው ቃል የሚያመላክተው “ከተለመደው በላይ እና ባሻገር” መሆኑን ነው። ቦኤዝ ሩት ከነዶው ዙርያ እንድትቃርም ይፈቅዱ ዘንድ ለሰራተኞቹ ተዕዛዝ ይሰጣል። ብዙውን ግዜ የሚቃርሙ ሰዎች ወደ ነዶው እንዲጠጉ አይፈቀድም።

ከታሰረው ነዶ ላይ ጥቂት ጠቂቱን እየመዘዛቹ

“ከነዶው አስቀርታችሁ ተዉላት” ወይንም “ከነዶው ላይ የ እህሉን ዘለላ ወስዳችሁ ተዉላት”

አታስቀይሟት

“አታሳፍሯት” ወይንም “አታዋርዷት”

Ruth 2:17

ወቃችው

የሚበላውን የእህሉን ክፍል ከገለባው ለየችው።

የእህሉ ዘለላ

ይሄ የሚሰበሰበወሀል የሚበላው ፍሬ ክፍል ለው

አንድ የኢፍ መስፈሪያ

አንድ የኢፍ መስፈሪያ 22 ሊትር ያክላል። “22 ሊትር የሚያህል ገብስ”

ያንንም ይዛ ወደ ከተማው ሄደች

ሩት እህሉን ተሸክማ ወደቤቷ እንደሂአደች ያመላክታል።

አማቷ . . . አየች

“ኑኃሚን”

Ruth 2:19

ዛሬ የቃረምሽው ከየት ነው? የትስ ቦታ ስትሰሪ ዋልሽ?

ኑኃሚን የጠየቀችው ጥያቄ ተመሳሳይ ሲሆን፤ ሩት ስላሳለፈችው ቀን ለማወቅ እጅግ ጓጉታ እንደሆነ ያስታውቃል።

የተባረከ ይሁን

እግዚአብሔር ቦኤዝ ለሩት እና ለኑኃሚን ስላሳያቸው ቸርነት እንዲባርካቸው እየጠየቀች ነው።

በጎነቱን . . . ያልተወ

“ታማኝነቱን ያልተወ” ትርጉሙ ሊሆን የሚችለው 1) ቦኤዝ እንደቤተሰብ ለኑኃሚን ያለበትን ኃላፊነት አስታውሷል። 2)ኑኃሚን በቦኤዝ ውስጥ ስራን እየሰራ ያለውን እግዚአብሔር ማለቷ ነው። 3) እግዚአብሔር ለሕያዋን እና ለሙታን ታማኝነቱን መጠበቁን ላማመልከት ነው።

ለሕያዋን

“በሕይወት ላሉ ሰዎች ሁሉ።” ኑኃሚን እና ሩት “ሕያዋን” ነበሩ።

ለሙታን

የኑኃሚን ባል እና ልጆች “ሞተው” ነበር። “ሙታን” የሚለውን ቃል ሊተካ የሚችል ሌላ ተተኪ ቃል ካለ እርሱን መጠቀም ይቻላል።

ዘመዳችን ነው፤ የመቤዠት ግዴታ ካለባቸው

የሁለተኛው ስንኝ መጀመርያውን የደግመዋል ያሰፋዋልም። በዕብራውያን ይህ አትክሁሮት የመስጫ መንገድ ነው።

የመቤዠት . . . ዘመዶች

የሚቤዥ ዘመድ ማለት አንዲት መበለት የገንዘብ እና ሌላ ችግር ውስጥ እንዳትገባ አግብቶ አንድ ልጆች አብሯት ወልዶ የሚያድናት ማለት ነው።

Ruth 2:21

ደግሞም . . . ብሎኛል

“ደግሞ . . . አለኝ።” ይህ የሚያመላክተው ከዚህ በኋላ ቦኤዝ አለኝ የምትለው ነገር ጠቃሚ እንደሆነ ነው።

ከሰራተኞቼ አትለዪ

ቦኤዝ ሰራተኞቹ ሊሲጧት የሚችሉትን ጥበቃ ያመላክታል።

ብትወጪ

“መሄድ ስሻልሻል።”

ጉዳት ሊያገኝሽ

ለማለት ተፈልጎ የሚሆነው 1)ሌሎች ሰራኞች ሩትን ሊጎዷት ይችላሉ እጇንም ይዘው ሊደፍሯት ይችላሉ። 2)በሌሎች እርሻ የእርሻው ባለቤተስከ መኧር መጨረሻ ድረስ እንዳትቃርም ልትከለከል ትችላለጭ

Ruth 2:23

ተጠግታ

ሩትም እስከቀኑ መጨረሻ ድረስ በቦኤዝ እርሻ ስትሰራ ዋለች፤ ደንነቷም ተጠበቀ።

ከአማቷም ጋር ኖረች

ሩት ማታ ላይ ለመተኛት ወደ ኑኃሚን ቤት ትሄድ ነበር።


Chapter 3

1 አማትዋም ኑኃሚን ለእርስዋ “ልጄ ሆይ፣ ታርፊ ዘንድ፣ ነገሮችም ለአንቺ መልካም ይሆኑልሽ ዘንድ፣ የምታርፊበትን ስፍራ አልፈግልሽምን?” አለቻት፡፡ 2 አሁንም ቦዔዝ፣ ከወጣት ሴቶች ሰራተኞቹ ጋር የነበርሽበት ሰው፣ ዘመዳችን አይደለምን? ተመልከቺ፣ እርሱ ዛሬ ማታ በአውድማው ላይ ገብሱን በመንሽ ይበትናል፡፡ 3 ስለዚህ፣ ታጠቢ፣ ሽቶሽን ተቀቢ፣ ልብስሽን ቀይሪ፣ ወደ አውድማውም ውረጂ፡፡ ነገር ግን መብላትና መጠጣት እስኪጨርስ ድረስ ለሰውዮው አትታወቂ፡፡ 4 በተኛም ጊዜ፣ ወደ እርሱ መሄድ እንድትችይ እርሱ የተኛበትን ስፍራ ማስታወስሽን እርግጠኛ ሁኚ፣ እግሩን ግለጪ፣ በዚያም ተጋደሚ፡፡ ከዚያም የምታደርጊውን እርሱ ይነግርሻል፡፡ 5 ሩትም ለኑኃሚን “የተናገርሽኝን ሁሉ አደርጋለሁ” አለቻት፡፡ 6 ስለዚህ ወደ አውድማውም ወረደች፣ እርስዋም አማትዋ የሰጠቻትን ትዕዛዝ ተከተለች፡፡ 7 ቦዔዝም በበላና በጠጣ ጊዜ፣ ልቡም ደስ ባለው ጊዜ፣ በእህሉ ክምር ጫፍ ሊተኛ ሄደ፡፡ ከዚያም ሩት በቀስታ መጣች፣ እግሩንም ገለጠች፣ ተኛችም፡፡ 8 እኩለ ሌሊት በሆነ ጊዜ ሰውዮው ደነገጠ፡፡ እርሱም ዘወር አለ፣ አንዲትም ሴት እዚያው እግርጌው ተኝታ ነበረች፡፡ 9 እርሱም “ማን ነሽ? አለ፡፡ እርስዋም “እኔ ሴት አገልጋይህ ሩት ነኝ” አለችው፡፡ አንተ የቅርብ ዘመዴ ነህና ልብስህን በሴት አገልጋይህ ላይ ዘርጋ አለችው፡፡ 10 ቦዔዝም፣ “ልጄ ሆይ፣ በእግዚአብሔር የተባረክሽ ሁኚ፡፡ ከመጀመርያው ይልቅ በመጨረሻ ብዙ ደግነት አሳይተሻል፣ ምክንያቱም ድሃም ይሁን ባለጠጋ ከወጣት ወንዶች ከአንዳቸውም ጋር አልሄድሽምና” አላት፡፡ 11 አሁንም፣ ልጄ ሆይ፣ አትፍሪ! ያልሽውን ሁሉ አደርግልሻለሁ፣ ምክንያቱም በከተማየ ያሉ ሕዝብ ሁሉ ምግባረ መልካም ሴት እንደ ሆንሽ ያውቃሉ፡፡ 12 አሁን እኔ የቅርብ ዘመድ መሆኔ እውነት ነው፤ ይሁን እንጂ ከእኔ የበለጠ የሚቀርብ ዘመድ አለ፡፡ 13 ዛሬ ሌሊት እዚህ ቆዪ፣ ነገም ጠዋት የዋርሳነትን ግዴታ እርሱ የሚፈጽም ከሆነ፣ መልካም ነው፣ የዋርሳነትን ግዴታ ይፈጽም፡፡ ነገር ግን እርሱ ለአንቺ የዋርሳነትን ግዴታ ባይፈጽም፣ ሕያው እግዚአብሔርን እኔ አደርገዋለሁ፡፡ እስከ ማለዳ ድረስ ተኚ፡፡ 14 ስለዚህ እስከ ማለዳ ድረስ በእግርጌው ተኛች፡፡ ነገር ግን አንዱ ሌላውን ማወቅ ከመቻሉ በፊት ተነሳች፡፡ ቦዔዝ “ሴት ወደ አውድማው መምጣትዋን ማንም እንዳያውቅ” ብሎ ነበርና፡፡ 15 ከዚያም ቦኤዝ “የለበስሽውን ልብስ አምጭና ያዢው” አላት፡፡ በያዘችም ጊዜ ስድስት ትልቅ መስፈሪያ ገብስ በልብሷ ላይ ሰፍሮ አሸከማት፡፡ የዚያን ጊዜ እርሱ ወደ ከተማ ሄደ፡፡ 16 ሩት ወደ አማትዋ በመጣች ጊዜ “ልጄ ሆይ፣ እንዴት ነሽ?” አለቻት፡፡ ሩትም ሰውዮው ለእርስዋ ያደረገውን ሁሉ ነገረቻት፡፡ 17 እርስዋም “እነዚህ ስድስት መስፈሪያ ገብስ እርሱ የሰጠኝ ናቸው፣ ‘ወደ አማትሽ ባዶ እጅሽን አትሂጂ’” ብሏልና፡፡ 18 ኑኃሚንም “ልጄ ሆይ፣ ይህ ጉዳይ እንዴት እንደሚሆን እስከምታውቂ ድረስ በዚህ ቆዪ፣ ሰውዮው ይህን ነገር ዛሬ እስኪጨርስ ድረስ አያርፍምና” አለች፡፡



Ruth 3:1

አማቷ

ኑኃሚን የሩት ሟች ባል እናት ናት

ልጄ

ሩት የኑኃኒንን ልጅ በማግባት ብሎም አብራት ወደ ቤተልሔም በመመለስ የኑኃሚን ልጅ ሆናለች።

የሚመችሽን ቤት እንድፈልግልሽ አይገባኝምን?

“መልካም እንዲሆንልሽ እረፍት አልፈልግልሽም?” ኑኃሚን ይሄንን ጥያቄ በመጠየቅ ያቀደችላትን ለመናገር ትጠቀምበታለች። “እረፍት የመታረጊበትን ቦታ ልፈልግልሽ ይገባኛል” ወይንም “ የሚንከባከብሽ ባል ልፈልግልሽ ይገባኛል።”

የምታርፊበት ቦታ

ትርጉሙ ሊሆን የሚችለው፤ 1) በቀጥታ የምትኖርበትን ቤት ማግኘት ወይንም 2) በማስጠጋት ረገድ የሚንከባከባት ባል ስለመፈለግ። ኑኃሚን ሁለቱንም ማለት ፈልጋ ሊሆንም ይችላል።

ከሴቶች ሠራተኞቹ ጋር አብረሽ የነበርሽበት

የዚህ ግልፅ ትርጉም ከሴቶቹ ጋር እየሰራች እንደነበረ ሊያሳይ ይገባል። “ከገረዶቹ ጋር የለበርሽበት።”

ዘመዳችን አይደለምን?

ኑኅሚን ከዚህ በፊት ለሩት የነገረቻትን ነገር እያስታወሰቻት ነው የሚሆነው። “እርሱ ዘመዳችን ነው።”

አሁንም

“ልብ በይ።” ከዚህ በኋላ የምትላትን ነገር እንድታስተውል እያመለከቻት ነው።

ያበራል

“በመንሽ ይበትናል” ይህ በንፍስ ድጋፍ ሰብሉን ከገለባው የመለየት ሂደት ነው።

Ruth 3:3

ሽቶ ተቀቢ

ይህ መልካም ማዓዛ ያለው ጣሳጭ ሻታ ያለው ዘይት ሊሆን ይችላል። በሁን ግዜ ሽቶ የሚባለው ማለት ነው።

ወደ አውድማው ውረጂ

ይህ የሚያሳየው ከከተማው ወጥቶ ወደሚወቃበት ቦታ ምሄድን ነው።

እግሩን ገልጠሽ

ይህ የሚያመላክተው የለበሰውን መደረብያ እግሩ ጋር መግለጥ እና እግሮቹ እንዲበርዳቸው ማድረግ የሚለውን ነው።

ተኚ

“ከእግሩ ሳር ተኚ”

ከዚያም የምታደርጊውን ራሱ ይነግርሻል

እዚህ ጋር ያለው የባህል ልማድ በእርግጥ ባይታወቅም፤ በባህላሸው የሚታወቅ እና ተቀባይነት ያለው ሴት ልጅ አንድ ወንድ እንዲያገባት ፈቃደኛ እንደሆነች የምታስታውቅበት መንገድ ነው። ቦኤዝም ልማዱ ገብቶት መቀበልም መተውም ይሽላል።

ይነግረሻል

“ሲነሳም፣ እርሱ እራሱ።”

ደስም ከተሰኘ

ይህ በልቡ የሆነ ነገርን ያሳያል። ሰክሮ ነበር ማለት አይደለም። “ሰውነቱም ደስ ከተሰኘ” ወይንም “ከረካ በኋላ”

በቀስታ

“በድብቅ” “ድምጽ ሳታሰማ ማንም ሰው ሳይሰማ”

እግሩንም ገልጣ

“መደረብያውን ከእግሩ ላይ ገልጣ”

ተኛች

“ከእግሩ ስር ተኛች”

Ruth 3:8

እንዲህም ሆነ

በትረካው ውስጥ የሆነን አንደ ክስተት ለማስታወቅ የሚጠቅም ስንኝ ነው። በቋንቋችሁ ይህንን የሚያደርግ ቃል ካለ እርሱን መጠቀምን አስቡ።

እኩለ ሌሊት ላይ

“መንፈቀ ሌሊትም በሆነ ግዜ”

ደነገጠ

“አንዳች ነገር አስደነገጠው”

ገልበጥ ሲልም

“ዘወርም አለ”

አንዲት ሴት እገርጌው ተኝታ አገኘ

ሲቲቱ ሩት ነበረች፤ ቦኤዝ ግን ጨልሞ ስለነበር ሊያውቃት/ሊለያት አልቻለም።

አገልጋይህ

ሩት ለቦኤዝ ምላሽ የሰጠችው በትህትና ነበር

ልብስህን ጣል አርግብኝ

ይህ ጋብቻን የሚያመላክት አባባል ነው።

ቅርብ የስጋ ዘመድ

ለዘመዶቹ ኃላፊነት ያለበት ልዩ ዘመድ

Ruth 3:10

ልጄ

ቦኤዝ ይህንን የተጠቀመው ታናሹ እንዳሆነች ሴት ለሩት ያለውን አክበሮት ነው።

ከዚህ በፊት ካደረግሽው ይልቅ ያሁኑ በጎነትሽ ይበልጣል

“ከበፊተኛው ይልቅ በመጨረሻው ግዜ ቸርነት አድርገሻል።”

በመጨረሻው ግዜ ቸርነት

ይህ ሩት ቦኤዝ እንዲያገባት ስለመጠየቁ ነው። የኑኃሚንን ዘመድ በማግባት ሩት ለኑኃሚን የሚያስፈልጋትን ነገር ማቅረብ ትችላለች በዚህም ቸርነትን ታደርጋለች።

ከዚህ በፊት

ይህ የሚያሳየው ሩት ከዚህ በፊትም ለአማቷ እየቃረመች እንደተንከባከበቻት እና አብራት በለቆየት ያደረገችውን ነው።

ፈልገሽ አልሄድሽምና

“አልተከተልሽምና” ሩት ኑኃሚንን ዘንግታ ከኑኃሚን ዘመዶች ውጪ ለማግባት ባል መፈለግ ስትችል ይህንን አላደረገችም።

Ruth 3:12

ከእኔ ይልቅ . . . ቅርብ የስጋ ዘመድ

መበለቲቷን መርዳት ቅርብ የሆነው ወንድ ዘመድ ኃላፊነት ነው።

ሊቤዥሽ ከፈለገ

ቦኤዝ እየተናገረ ያለው ቅርብ ከሆነ ከሞተው የሩት ባል የስጋ ዘመድ የሚጠበቀውን ሩትን የማግባት እና የቤተሰቡን ስም የዞ የመቀጠል ሃላፊነት ነው።

በሕያው እግዚአብሔር

“ሕያው እግዚአብሔርን” ይህ በዕብራይስጥ የተለመደ መሃላ ነው።

Ruth 3:14

እግርጌው ተኛች

ሩት ከቦኤዝ እግር ስር ተኛች። ቦኤዝ አላወቃትም፣ ምንም አላደረጉም።

ሰው ተለይቶ ሊታወቅ በማይችልበት ሰዓት

ይህን አገላለፅ ከበርሃን ጋር አያይዞ መግለፅ ይቻላል። “ገና ጨለማ ሳለ”

የደረብሽውን ልብስ

በትከሻ ላይ የመደረብ ልብስ

ስድስት መስፈርያ ገብስ

ክብደቱ በውል ባይገለፅም። ቸር የሆነ ልገሳ እንደሆነ ይገመታል፣ ነገር ግን ሩት ልትሸከመው የምትችለው ያህል።

አሸከማት

የገብሱ መጠን ሩት በራስዋ ልታነሳው የምትችለው ያክል አልነበረም።

እርሱም ወደከተማይቱ ሄደ

“ወደ ከተማ ተመለሰች” አንዳንድ ቅጂዎች “ተመለሰ” ሲሉ ሌሎች ደግሞ “ተመለሰች” ይሉታል።

Ruth 3:16

የሄድሽበት ጉዳይ እንዴት ሆነ

ኑኃሚን በዚህ ጥያቄ ማለት የፈለገችውን በሌላ ቃል ግልጽ ማድረግ ይቻላል። “ልጄ ምን ሆነ?” ወይንም “ቦኤዝ ምን ዓይነት ምላሽ ሰጠሽ?”

ሰውየው ያደረገላትን ሁሉ

“ቦኤዝ ያደረገላትን ሁሉ”

ባዶ እጅሽን አትመለሺ

“ባዶ እጅሽን አትሂጂ” ወይንም “ምንም ሳትይዢ እንዳትሄጂ” ወይንም “የሆነ ነገር የመሄድሽን እርገት፣ እኛ ሁኚ

እልባት ካላገኘ

ይህ ማን የኑኃሚንን ንብረት እንደሚገዛ እና ሩትን እንደሚያገባ የሚወሰነውን ውሳኔ ያመላክታል።

በር

“የከተማይቱ በር” ወይንም “የቤተልሔም በር” ይህ ቅጥር ወዳላት የቤተልሔም ከተማ ዋና መግቢያ በር ነው። የማህበረሰባዊ ጉዳዪች ላይ ውይይት የሚደረግበትም ክፍት ቦታ በበሩ አቅራብያ ነበር።

የቅርብ ዘመድ

በሕይወት ያላ ቅርቡ የአቤሜሌክ ዘመድ

ከከተማይቱ ሽማግሌዎች

“የከተማይቱ መሪዎች”


Chapter 4

1 ቦዔዝም ወደ ከተማይቱ በር ሄደና በዚያ ተቀመጠ፡፡ ወዲያውኑ ቦዔዝ ሲናገርለት የነበረው የቅርብ ዘመድ መጣ፡፡ ቦዔዝም ለእርሱ “ወዳጄ ሆይ፣ ና በዚህም ተቀመጥ” አለው፡፡ ሰውየውም መጣና ተቀመጠ፡፡ 2 ቦዔዝም ከከተማይቱ ሽማግሌዎች አሥር ሰዎች ወሰደ፣ “በዚህ ተቀመጡ” አላቸው፡፡ እነርሱም ተቀመጡ፡፡ 3 ቦዔዝም የቅርብ ዘመድ ለሆነው፣ “ከሞዓብ ምድር የተመለሰችው ኑኃሚን የወንድማችንን የአቤሜሌክን ቁራሽ መሬት ትሸጣለች፡፡ 4 እኔም ለአንተ አስታውቅህ ዘንድ አሰብሁ እንዲህም አልሁ፡- ‘ይህንን መሬት በዚህ በተቀመጡት በሕዝቤ ሽማግሌዎች ፊት ግዛው፡፡’ መቤዠት ብትፈልግ ተቤዠው፡፡ ነገር ግን መቤዠት የማትፈልግ ከሆነ ግን ከአንተ በቀር ሌላ የሚቤዥ የለምና፣ እኔም ከእአንተ በኋላ ነኝና እንዳውቀው ንገረኝ” አለው፡፡ የዚያን ጊዜ ሌላኛው ሰው “እቤዠዋለሁ” አለው፡፡ 5 ቦዔዝም “ከኑኃሚን እጅ እርሻውን በምትገዛበት ቀን፣ የሞተውን ሰው ስም በርስቱ ላይ እንድታስነሣለት የምዋቹን ሰው ሚስት ሞዓባዊቱን ሩትን ደግሞ መውሰድ አለብህ” አለ፡፡ 6 የቅርብ ዘመድ የሆነውም “የራሴን ርስት ሳልጎዳ እርሻውን ለራሴ መቤዠት አልችልም፡፡ እኔ ልቤዠው አልችልምና የእኔን የመቤዠት መብት ለራስህ ውሰድ” አለ፡፡ 7 በጥንት ዘመን መቤዠትና የሸቀጦች መለዋወጥ በተመለከተ በእስራኤል ዘንድ አንድ ልማድ ነበረ፡፡ ሁሉንም ነገር ለማጽናት ሰው ጫማውን ያወልቅና ለባልንጀራው ይሰጠዋል፤ በእስራኤል ውስጥ ሕጋዊ ስምምነት የሚኖረው በዚህ ሁኔታ ነበር፡፡ 8 ስለዚህ የቅርብ ዘመዱ ቦዔዝ፣ “አንተ ለራስህ ግዛው” አለው፡፡ እርሱም ጫማውን አወለቀ፡፡ 9 ቦዔዝም ለሽማግሌዎቹና ለሕዝቡ ሁሉ፣ “ለአቤሜሌክ የነበረውን ሁሉ እንደዚሁም ለኬሌዎንና ለመሐሎንም የነበረውን ሁሉ ከኑኃሚን እጅ እኔ መግዛቴን እናንተ ዛሬ ምስክሮች ናችሁ፡፡ 10 ከዚህም በላይ ስለ መሐሎን ሚስት ስለ ሞዓባዊቷ ሩት፡- የምዋቹን ሰው ስም በርስቱ ላይ እንዳስነሣ፣ ስሙ ከወንድሞቹ መካከልና ከአገሩም ደጅ እንዳይጠፋ፣ እኔ ደግሞ እርስዋ ሚስቴ እንድትሆን ወስጃታለሁ፡፡ እናንተም ዛሬ ምስክሮች ናችሁ” አላቸው፡፡ 11 በበሩ የነበሩ ሕዝብ ሁሉና ሽማግሌዎቹም እንዲህ አሉ፡- “እኛ ምስክሮች ነን፡፡ እግዚአብሔር ወደ ቤትህ የመጣችውን ሴት የእስራኤልን ቤት እንደ ገነቡት እንደ ሁለቱ እንደ ራሔልና ልያ ያድርጋት፡፡ አንተም በኤፍራታ ባለጠጋ ሁን፣ በቤተ ልሔምም እንደገና የታወቅህ ሁን፡፡ 12 ቤትህ እግዚአብሔር ከዚህች ወጣት ሴት በሚሰጥህ ዘር በኩል ትዕማር ለይሁዳ እንደወለደችለት እንደ ፋሬስ ቤት ይሁን” አሉት፡፡ 13 ስለዚህ ቦዔዝ ሩትን ወሰደ፣ ሚስቱም ሆነች፡፡ እርሱም ከእርስዋ ጋር ተኛ፣ እግዚአብሔርም ልጅ እንድትፀንስ ፈቀደላት፣ እርዋም ወንድ ልጅ ወለደች፡፡ 14 ሴቶችም ለኑኃሚን፣ “ዛሬ የሚቤዥ የቅርብ ዘመድ ያላሳጣሽ እግዚአብሔር ይባረክ፡፡ ይህ ሕጻን ስሙ በእስራኤል ውስጥ የገነነ ይሁን፡፡ 15 ይህ ልጅ ለአንቺ ሕይወትሽን የሚያድስ እርጅናሽንም የሚመግብ ይሁን፣ የምትወድሽ፣ ከሰባትም ወንዶች ልጆች ይልቅ ለአንቺ የምትሻል፣ ምራትሽ ይህን ልጅ ወልዳለችና፡፡ 16 ኑኃሚንም ሕፃኑን ወሰደችው፣ በእቅፍዋም አስቀመጠችው፣ እርሱንም ተንከባከበችው፡፡ 17 ጎረቤቶቿ የሆኑት ሴቶችም “ለኑኃሚን ወንድ ልጅ ተወለደላት” እያሉ ስም ሰጡት፡፡እነርሱም ስሙን ኢዮቤድ ብለው ጠሩት፡፡ እርሱም የዳዊት አባት የሆነው፣ የእሴይ አባት ሆነ፡፡ 18 አሁንም እነዚህ የፋሬስ ትውልድ ነበሩ፡- ፋሬስ የኤስሮም አባት ሆነ፣ 19 ኤስሮምም የአራም አባት ሆነ፣ አራምም የአሚናዳብ አባት ሆነ፣ 20 አሚናዳብም የነአሶን አባት ሆነ፣ ነአሶንም የሰልሞን አባት ሆነ፣ 21 ሰልሞንም የቦዔዝ አባት ሆነ፣ ቦዔዝም የኢዮቤድ አባት ሆነ፣ 22 ኢዮቤድ የእሴይ አባት ሆነ፣ እሴይም የዳዊት አባት ሆነ፡፡



Ruth 4:3

ኑኃሚን መሬት ልትሸጥ ነው።

ለቅርብ ዘመድ፤ የቤተዘመዱን መሬት የመግዛት እና ቤተሰቡን የመንከባከብ ኃላፊነት አለበት። አሁን ደግሞ ይህ ሰው የኑኃሚንን መሬት መግዛት፤ ሩትን ማግባት እና ኑኃሚንን መንከባከብ ይኖርበታል።

ፊት

ይህ የሚደረገውን ስምምነት ህጋዊ እና ፍፁም ያደርገዋል።

መቤዠት

ይህ ማለት መሬቱን መግዛት እና በቤተሰቡ ውስጥ እንዲቆይ ማድረግ ማለት ነው።

ከአንተ ቀጥሎ . . . ስለ ሆንሁ

ቦኤዝ በቀጣይነት መሬቱን ሊቤዥ የሚችለው ዘመድ እርሲ ነበር።

Ruth 4:5

በምትገዛበት ዕለጥ. . . አለብህ

በዚህ የቦኤዝ አነጋገር ለሰውዬው መሬቱን ከመግዛት ጋር አብሮ ያለውን ኃላኢነት ይነግረዋል።

ከኑኃሚን

“ከኑኃሚን እጀ” ይህ የሚያመለክተው መሬቱ የኑኃሚን መሆኑን ነው።

ሩትን አብረህ መውሰድ

“ሩትንም ማግባት”

የሟቹን ሚስት . . . ሩት

“ሩት የአቤሜሌክ ልጅ መበለት”

የሟቹን ስም . . . ለማስጠራት

“ንብረቱን የሚወርስ ወንድ ልጅ እንዲኖራት እና የሞተውን ባሏን ስም እንዲያስቀጠል።”

የራሴን ርስት አደጋ ላይ ሊጥል

ሩት ለምትወልድለት ልጆች ደግሞ የራሱን ሃብት ማካፈል ስለሚኖርበት

የኔን የሜቤዠት ስልጣን አንተ ውሰደው

“አንተው እራስህ ተቤዠው” ወይንም “በእኔ ፈንታ አንተ ተቤዠው።”

Ruth 4:7

ልማድ ነበረ

ጸሃፊው ሩት በነበረችበት ዘመን በልውውጥ ግዜ የሚደረገውን ነገር እያብራራ ነው።

በጥንት ግዜም

“በጥንት ዘመን።” ይህ የሚያመላክተው መጸሓፉ በተጻፈበት እና ታሪኩ በተፈፀመበት ግዜ ልማዱ እንደተለወጠ ነው።

ጫማውን

“ነጠላ ጫማውን።”

ለባልንጀራውም

ይህ የሚያመላክተው ከእርሱ ጋር ስምምነት እያደረገ ያለውን ሰው ነው። በዚህ ግዜ ቅርብ የስጋ ዘመድ የተባለው ሰው ለቦኤዝ እንደማለት ነው።

Ruth 4:9

ለሽማግሌዎቹ እና ለህዝቡ ሁሉ

ይህ ማለት በስብሰባቸው ላይ የነበሩት ሰዎች ሁሉ ማለት እንጂ በከተማው ያሉ ሰዎች ሁሉ ማለት አይደለም።

የአቤሜሌክን፣ የኬሌዎንን እና የመሓሎንን ንብረት በሙሉ

ይህ የሚያመላክተው የኑኃሚን ሟች ባል እና ልጆች ሃብት በሙላ ማለት ነው።

ከኑኃሚን

“ከኑኃሚን እጅ” ለንብረቱ ሁላ ኃላፉ የነበረችው እና የምትሰጠው ኑኃሚን ለመሆኗ ማሳያ ነው።

የሟቹን ስም በርስቱ ላይ ለማስጠትራት

ሩት የምትወልደው የመጀመርያ ልጅ ህጋዊ የመሓሎን ልጅ ተደርጎ ይቆጠራል። ቦኤዝም ከኑኃሚን የገዛውን መሬት ይወርሳል። “የሞተውን ሰውዬ መሬት የሚወርስ ወንድ ልጅ እንድሰጣት።”

የሟቹ ስም ከወንድሞቹ መካከል ከአገሩ ደጅ እንዳይጠፋ

መረሳት የሚታየው ቀድሞ ይኖሩ ከነበሩ ሰዎሽ ስም ዝርዝር እንደመቆረጥ ነው። “በወንደሞቹ ትውልድ ዘንድ እና በከተማው እንዳይረሳ።”

ከአገሩ ደጅ

ይህ የሚያመላክተው የከተማውን ደጅ ሲሆን፤ በዚህም ቦታ የመሬት ባለቤትነትን በተመለከተ ውሳኔ የሚሰጥበት ቦታ ነው።

Ruth 4:11

በከተማይቱ በር የነበሩ ሁሉ

“ሌሎች በበር አቅራብያ ይሰበሰቡ የነበሩ ሁሉ።”

ወደ ቤትህ የምትገባውን

ይህ ምሳሌያዊም ቀጥተኛም ትርጉም አለው። ሩት ቦኤዝን ስታገባው ወደቤቱ ትገባለጭ ቤት መግባት ማለት ደግሞ ቤተሰቡን መቀላቀልንም ያመላክታል።

እንደ ራሔል እና ልያ

እነኚህ የያዕቆብ ሁለት ሚስቶች ሲሆኑ ስማቸውም ወደ እስራኤል ተቀይሯል።

የእስራኤልን ቤት እንደሰሩ

“ብዙ ልጆችን ወልደው የእስራኤል ሐዝብ ያደረጉ።”

በኤፍራታ የበረታ

ኤፍራታ ቦኤዝ በቤተንሔም የሚነኝበት ነገድ ነው።

ቤትህ እንደ

እግዚአብሔር ይሁዳን በልጁ በፋሬስ እጅጉን ባርኮት ነበር፤ ሰዎቹም በተመሳሳይ መንገድ ቦኤዝን በሩት ልጆች እንዲባርከው እግዚአብሔርን ጠየቁጥ

ትዕማር ለይሁዳ እንደወለደችው

ተዕማር መበለት ነበረች። ይሁዳም ከእርሷ ወንድ ልጅ ወለደ፤ የቤተሰቡም ስም በዛ ቀጠለ።

እግዚአብሔር . . . በሚሰጥህ ዘር

እግዚአብሔር በሩት በኩል ልጅ እንደሚሰጠው

Ruth 4:13

ቦኤዝ ሩትን ወሰዳት

“ቦኤዝ ሩትን አገባት” ወይንም “ቦኤዝ ሩትን እንደ ሚስት ወሰዳት”

ወደ እርሷ ገባ

ቦኤዝ ሩትን እንዳወቃት የሚያሳይ ነው። “ቦኤዝ ሩትን ደረሰባት”

ቅርብ የስጋ ዘመድ ያላሳጣሽ

አዎንታዊ ትርጉም ሊሰጠው ይችላል። “ዛሬ የቅርብ ዘመድ የሰጠሽ”

ስሙ ይግነን

ይሄ የሚያመላክተው የኑኃሚንን የልጅ ልጅ ዝና እና ባህርይ ነው።

ሕይወትሽን ያድሳታል

ኑኃሚን በልጅ ልጇ ምክኛት እንዴት በድጋሚ ደስታን እና ተስፋን እንደምትለማመድ ሊያሳይ ይችላል። “ድስታን በድጋሚ ወደ አንቺ የሚያመጣ” ወይንም “በድጋሚ እንደ ወጣት የሚያበረታሽ።”

በእርጅና ዘመንሽም ይጦርሻል

“ባረጀሽ ግዜ የሚንከባከብሽ።”

ከሰባት ወንድ ልጆች የምትበልጥ

በእስራኤላውያን “ሰባት” የፍፁምነት ቁጥር ነው። የኑኃሚን ወንድ ልጆች ሳይወልዱላት ሞቱ፤ ሩት ግን ከቦኤዝ የልጅ ልጅ ወለደችላት። “ከምንም ዓይነት ልጅ የምትሻል።”

Ruth 4:16

ኑኃሚን ልጁን ተቀብላ

ሉጁን እንደያዘችው እንጁ ከሩት እንደወሰደችባት መታየት የለበትም።

ታቀፈችው

“ከደረቷ አስጠግታ ያዘችው።”የሄ የፍቅር እና መውደድ ማሳያ ነው።”

ለኑኃሚን ወንድ ልጅ ተወለደላት

“ልጁ ለኑኃሚን እንደልጇ ነው።” ኑኃሚን ልጁን ባትወልደውም የእርሷ የልጅ ልጅ እንደሆነ የታወቀ ነበር።

የዳዊት አባት

“የንጉስ ዳዊት አባት።” ንጉስ የሚለው ያልተጠቀሰው የመጀመርያዎቹ አንባብያን ዳዊት ንጉስ እንደነበረ ስለሚረዱ ነው።

Ruth 4:18

የፋሬስ ቤተሰብ ትውልድ

“ከእርሱ የወጡት ትውልዶች።” ከፋሬስ የተለሳበት ምክንያት ከዚህ በፊት ፋሬስ የይሁዳ ልጅ መሆኑ ስለተገለጠ ነው፤ ከእርሱም ቀጥሎ የቤተሰቡን ዝርዝር መናገር የቀጥላል።


Book: 1 Samuel


1 Samuel

Chapter 1

1 በተራራማው በኤፍሬም አገር በራማ መሴፋ የሚኖር አንድ ሰው ነበር፤ ስሙ ሕልቃና ይባላል፥ እርሱም የኤፍሬማዊው የናሲብ ልጅ፥ የቶሑ ልጅ፥ የኤሊዮ ልጅ፥ የኢያርምኤል ልጅ ነበር። 2 እርሱም ሁለት ሚስቶች ነበሩት፤ ስማቸውም የአንደኛዋ ሐና፥ የሁለተኛዋም ፍናና ነበር። ፍናና ልጆች ነበሯት፣ ሐና ግን አንድም ልጅ አልነበራትም። 3 ይህም ሰው በየዓመቱ ለሠራዊት ጌታ ለእግዚአብሔር ለመስገድና መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ ሴሎ ይሄድ ነበር። የእግዚአብሔር ካህናት የሆኑት ሁለቱ የኤሊ ወንዶች ልጆች አፍኒንና ፊንሐስ በዚያ ነበሩ። 4 በየዓመቱ ሕልቃና የሚሠዋበት ጊዜ ሲደርስ፥ ለሚስቱ ፍናና፥ ለወንዶችና ሴቶች ልጆችዋ በሙሉ ሁልጊዜ ከመሥዋዕቱ ሥጋ ድርሻቸውን ይሰጣቸው ነበር። 5 ነገር ግን ሐናን ይወዳት ስለነበር ሁልጊዜም ድርሻዋን ሁለት ዕጥፍ አድርጎ ይሰጣት ነበር፤ እግዚአብሔር ግን ማኅፀንዋን ዘግቶት ነበር። 6 እግዚአብሔር ማኅፀንዋን ዘግቶት ስለነበር ጣውንቷ እርስዋን ለማስመረር ክፉኛ ታስቆጣት ነበር። 7 ስለዚህ በየዓመቱ ወደ እግዚአብሔር ቤት ከቤተሰብዋ ጋር በምትወጣበት ጊዜ ጣውንቷ ሁልጊዜ ታበሳጫት ነበር። በዚህ ምክንያት ታለቅስ ነበር፤ ምግብም አትበላም ነበር። 8 ባሏ ሕልቃና ሁልጊዜ "ሐና ሆይ፥ ለምንድነው የምታለቅሽው? ምግብስ የማትበዪው ለምንድነው? ልብሽ የሚያዝነውስ ለምንድነው? ከዐሥር ወንዶች ልጆች ይልቅ ላንቺ እኔ አልሻልም?" ይላት ነበር። 9 ከእነዚህ ወቅቶች በአንዱ፥ በሴሎ መብላታቸውንና መጠጣታቸውን ከጨረሱ በኋላ ሐና ተነሣች። ካህኑ ዔሊ በእግዚአብሔር ቤት መግቢያ በራፍ በወንበሩ ላይ ተቀምጦ ነበር። 10 እርሷም እጅግ አዝና ነበር፤ ወደ እግዚአብሔር ጸለየች፥ አምርራም አለቀሰች። 11 እንዲህ ስትልም ስዕለት ተሳለች፣ "የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፥ የአገልጋይህን ጉስቁልና ብትመለከትና ብታስበኝ፥ አገልጋይህን ባትረሳኝ፥ ነገር ግን ወንድ ልጅን ብትሰጠኝ፥ እኔም የሕይወት ዘመኑን ሁሉ ለእግዚአብሔር እሰጠዋለሁ፥ መቼም ቢሆን ጸጉሩ አይላጭም"። 12 በእግዚአሔር ፊት ጸሎቷን ቀጥላ እያለች ዔሊ አፏን ይመለከት ነበር። 13 ሐና በልቧ ትናገር ነበር። ከንፈሮችዋ ይንቀሳቀሱ ነበር፥ ድምፅዋ ግን አይሰማም ነበር። ስለዚህ ዔሊ ሰክራለች ብሎ አሰበ። 14 ዔሊም "ስካርሽ የሚቆየው እስከ መቼ ነው? ወይንሽን ከአንቺ አርቂው" አላት። 15 ሐናም፣ "ጌታዬ ሆይ፥ አይደለም፥ እኔ ልቤ በሐዘን የተጎዳብኝ ሴት ነኝ። ወይን ወይም የሚያሰክር መጠጥ አልጠጣሁም፥ ነገር ግን ነፍሴን በእግዚአብሔር ፊት እያፈሰስኩ ነው። 16 አገልጋይህን እንደ ኃፍረተ ቢስ ሴት አትቁጠረኝ፤ ይህን ያህል ጊዜ የተናገርኩት እጅግ ከበዛው ሐዘኔና ጭንቀቴ የተነሣ ነው" በማለት መለሰችለት። 17 ከዚያም ዔሊ፣ "በሰላም ሂጂ፤ የእስራኤል አምላክ የለመንሽውን ልመና ይስጥሽ" ብሎ መለሰላት። 18 እርሷም፣ "አገልጋይህ በዐይንህ ፊት ሞገስን ላግኝ" አለችው። ከዚያም መንገዷን ሄደች፥ በላችም፤ ከዚያም በኋላ ፊቷ ሐዘንተኛ አልሆነም። 19 እነርሱም ማልደው ተነሥተው በእግዚአብሔር ፊት ሰገዱ፥ ከዚያም ወደ መኖሪያቸው ወደ አርማቴም ተመለሱ። ሕልቃና ከሚስቱ ከሐና ጋር ተኛ፥ እግዚአብሔርም አሰባት። 20 ጊዜው ሲደርስም ሐና አረገዘችና ወንድ ልጅ ወለደች። "ከእግዚአብሔር ስለ እርሱ ለምኜ ነበር" ስትል ስሙን ሳሙኤል ብላ ጠራችው። 21 ሕልቃናና ቤተ ሰቡ በሙሉ ለእግዚአብሔር ዓመታዊውን መሥዋዕት ለማቅረብና ስዕለታቸውን ለመፈጸም ዳግመኛ ወደ ሴሎ ወጡ። 22 ሐና ባሏን "ልጁ ጡት መጥባት እስኪያቆም እኔ አልሄድም፤ ከዚያም በእግዚአብሔር ፊት እንዲታይና ለዘላለም በዚያ እንዲኖር አመጣዋለሁ" ብላው ስለነበረ አልሄደችም። 23 ባሏም ሕልቃና፥ "መልካም መስሎ የታየሽን አድርጊ። ጡት መጥባቱን እስኪያቆም ቆዪ፥ ብቻ እግዚአብሔር ቃሉን ያጽና" አላት። ስለዚህ ልጇ ጡት መጥባቱን እስኪያቆም ድረስ በቤት በመቆየት ተንከባከበችው። 24 ጡት መጥባቱን ባስቆመችው ጊዜ፥ እርሱን ከሦስት አመት ወይፈን፥ አንድ ኢፍ ዱቄትና አንድ ጠርሙስ ወይን ጋር በሴሎ ወደሚገኘው ወደ እግዚአብሔር ቤት ወሰደችው። ልጁ ገና ሕፃን ነበር። 25 ወይፈኑን አረዱት፤ ልጁንም ወደ ዔሊ አመጡት። 26 እርሷም፥ "ጌታዬ ሆይ፥ ሕያው እንደመሆንህ፥ እዚህ አጠገብህ ቆማ ወደ እግዚአብሔር የጸለየችው ሴት እኔ ነኝ። 27 ስለዚህ ልጅ ጸለይኩኝ፥ እግዚአብሔርም የለመንኩትን ልመና ሰጥቶኛል። 28 ለእግዚአብሔር ሰጥቼዋለሁ፤ በሕይወት በሚኖርበት ዘመን ሁሉ ለእግዚአብሔር የተሰጠ ይሆናል"። እነርሱም በዚያ ለእግዚአብሔር ሰገዱ።



1 Samuel 1:1

አርማቴም

ይህ የአንዲት ትንሽ መንደር ስም ሲሆን ከኢየሩሳሌም በሰሜን ምዕራብ ስምንት ኪሎ ሜትር ያህል ርቃ የምትገኝ ሳትሆን አትቀርም፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

መሴፋ

ይህ የመሴፍ ትውልድ የሆኑ የሰዎች ስብስብ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

ሕልቃና … ኢያሬም … ኢሊዩ … መሴፍ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

ፍናና

ይህ የአንዲት ሴት ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

1 Samuel 1:3

ያም ሰው

"ያም ሰው' የሚለው ሕልቃናን ያመለክታል፡፡

ያህዌ

ይህ እርሱ በብሉይ ኪዳን ለሕዝቡ የገለጠው የእግዚአብሔር ስም ነው፡፡ ያህዌን በሚመለከት እንዴት እንዴት እንደሚተረጎም የትርጉም ቃላት ገጽን ተመልከት፡፡

ዔሊ፣ አፍኒንና ፊንሐስ

እንዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

1 Samuel 1:5

ሐና

ይህ የአንዲት ሴት ስም ነው፡፡ ይህንን በ1 ሳሙኤል 1፡2 እንዴት እንደምትተረጉም ተመልክት፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት፡፡)

ማኅፀንዋን ዘግቶ ነበር

"መካን አድርጓት ነበር' ወይም "ወደ እርግዝና እንዳትመጣ አግዷት ነበር'

ተፎካካሪዋ በጣም ታበሳጫት ነበር

ሌላኛዋ ሚስት (ጣውንትዋ) ሐናን ብዙ ጊዜ ታሳዝናትና ታዋርዳት ነበር

1 Samuel 1:7

ተፎካካሪዋ

የሕልቃና ሌላኛዋ ሚስት ፍናና ነች፡፡ ተፎካካሪ ማለት ሌላውን ሰው በመቃወም የሚወዳዳር ሰው ማለት ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ሕልቃና አብልጦ እንዲወዳት ፍናና ሐናን በመቃወም ትወዳደራት ነበር፡፡

ሐና ሆይ ለምን ታለቅሻለሽ? ለምንስ አትቀምሽም? ለምንስ ልብሽ ያዝንብሻል? እኔስ ከአሥር ልጆች አልሻልልሽምን?

አስፈላጊ ከሆነ አሳብ ገላጭ ጥያቄዎች በገላጭ አባባል ሊተረጎሙ ይችላሉ፡፡ አት፡- "ሐና ማልቀስ የለብሽም፡፡ እኔ ለአንቺ ከአሥር ልጆች ይልቅ ስለምሻልሽ ልትበይና ልብሽም ደስ ሊለው ይገባል፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄዎች ተመልከት)

ከአስር ልጆች ይልቅ

ሐና ምን ያህል ለእርሱ አስፈላጊ እንደሆነች አጽንዖት ለመስጠት ሕልቃና አጋኖ እየተናገረ ነው፡፡ አት፡- "ማንኛውም ልጅ ሊሆነው ከሚችለው በላይ' (ግነትና ማጠቃለያ ተመልከት)

1 Samuel 1:9

አጠቃላይ መረጃ

ሐና ወደ እግዚአብሔር መጸለይ ጀመረች ዔሊም ተመለከታት፡፡

በኋላም ሐና ተነሣች

ግልጽ ያልሆነ መረጃ በዚህ ስፍራ ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ ወይ የሐና ድንኳን ከመገናኛው ድንኳን ቀጥሎ ነበር ወይም ለመጸለይ ከድንኳንዋ ወደ መገናኛው ድንኳን ሄዳ ነበር፡፡ አት፡- "በኋላም ሐና ተነሣች ለመጸለይም ወደ እግዚአብሔር ቤት ሄደች፡፡' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ይልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ካህኑም ዔሊ

"ም' የሚለው ቃል እየተተረከ የዋናው ታሪክ ፍሰት መቋረጡን ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ በዚህ ስፍራ ጸሐፊው በታሪኩ ስለሌላ አንድ ሰው ይነግረናል፡፡ ይህም ሰው ካህኑ ዔሊ ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

የእግዚአብሔር መቅደስ

"መቅደሱ' በእርግጥ ድነኳን ነበር ነገር ግን ሕዝቡ ያመልክበት የነበረ ስፍራ ስለ ነበር፣ በዚህ ስፍራ መቅደስ ብሎ መተረጎም ይበልጥ የተመረጠ ነው፡፡

በልባዋ ትመረር ነበር

ምንም ልጆች ስለሌላትና የባሏ ሌላኛዋ ሚስቱ ፍናና ያለማቋረጥ ታዋርዳት ስለነበር ሐና እጅግ ትታወክና ታዝን ነበር፡፡ (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትንና ያልተገለጸ መረጃን ተመልከት)

1 Samuel 1:11

አያያዥ አሳብ

ሐና ወደ እግዚአብሔር የምታደርገው ጸሎት ቀጠለ፡፡

የባርያህን መከራ

መከራ የሚለው የነገር ስም በማሰሪያ አንቀጽ ሐረግነት ሊተረጎም ይችላል፡፡ ይህ የሚከተሉትን ሊያመለክት ይችላል፡- 1) የሐናን ማርገዝ አለመቻል፡፡ አት፡- "ማርገዝ ካለመቻሌ የተነሣ ምን ያህል መከራ እየተቀልኩ ነው' ወይም 2) ፍናን እርሷን ሁል ጊዜ የምታዋርድበትን መንገድ፡፡ አት፡- "ያቺ ሴት ምን ያህል መከራ እያሳየችኝ አንደሆነ' (የነገር ስሞች ተመልከት)

አስበኝ

እግዚአብሔር ስለ ሐና እርምጃ እንዲወስድ የቀረበ የተለየ ልመና ነው፡፡ ሐና ላይ ምን እየሆነባት እንዳለ እግዚአብሔረ ያውቃል፣ አልረሳም፡፡

ባርያህን አትርሳ

ይህ ሐረግ የሚለው ነገር "አስበኝ' ከሚለው ጋር ተመሣሣይ ነው ማለት ይቻላል፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

1 Samuel 1:12

ዔሊ ይመለከታት ነበር

ዔሊ ሊቀ ካህናት ነበር፣ በመሆኑም በእግዚአብሔር መገናኛ ድንኳን ነበረ በእርሷም ኃላፊነት ነበረበት፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

1 Samuel 1:15

እኔስ ልባዋ ያዘነባት ሴት ነኝ

"እኔ እጅግ ያዘንኩ ሴት ነኝ፡፡'

በእግዚአብሔር ፊት ነፍሴን አፈሰስሁ

ይህ "ጥልቅ የሆነ ስሜቴን ለእግዚአብሔር እየነገርኩ ነኝ' የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ባሪያህን እንደ … አትቁጠር

ሐና ትህትናዋን ለማሳየት ስለ ራሷ በሁለተኛ መደብ ተውላጠ ስም ትናገራለች፡፡ በአንደኛ መደብ ተውላጠ ስም ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "ባርያህን እንደ … አትቁጠረኝ' ወይም "አትቁጠረኝ' (አንደኛ፣ ሁለተኛ እና ሦሥተኛ መደብ ተመልከት)

ከጭንቀቴና ከብስጭቴ ብዛት እስከ አሁን ተናግሬአለሁ

እንደ 1፡15፣ ሐዘንተኛ ልብ እንዳላት የተነገረ ሌላ የአባባል መንገድ ነው፡፡ ብዛት፣ ጭንቀት እና ብስጭት የሚሉት የነገር ስሞች በቅጽልነት እና በማሰሪያ አንቀጽነት ሊተረጎሙ ይችላሉ፡፡ አት፡- "እስካሁን የተናገርኩት በጣም ስላዘንኩና ተፎካካሪዬ እጅግ ስላበሳጨችኝ ነው፡፡' (የነገር ስም ተመልከት)

ጭንቀትና ብስጭት

እነዚህ ሁለቱም ቃላት ተፎካካሪዋ ታበሳጫት ስለነበር ሐና ታዝንና ትናደድ ነበር የሚል ትርጉም አላቸው፡፡ (የሁለት ነገሮች ተመሳሳይነት ተመልከት)

ጭንቀት

ፍናና ታስቆጣትና ታናድዳት ነበር፡፡

ብስጭት

ፍናና ክፉ ስለሆነችባት ሐና ይሰማት የነበረውን የሐዘንና የውርደት ስሜት እያመለከተች ነው፡፡

1 Samuel 1:17

ዔሊም … መለሰላት

ዔሊ በማደሪያው ድንኳን የሚኖር ሊቀ ካህናት ነበር፡፡

ባርያህ … ታግኝ

ለሊቀ ካህናቱ ለዔሊ ያላትን አክብሮት ለማሳየት ሐና ራስዋን በሁለተኛ መደብ ተውላጠ ስም ትተራለች፡፡ ይህ በአንደኛ መደብ ተውላጠ ስም ሊተረጎም ይችላል፡፡ (አንደኛ፣ ሁለተኛ እና ሦሥተኛ መደብ ተመልከት)

በዓይንህ ፊት ሞገስ ላግኝ

በዚህ ስፍራ "ሞገስ ላግኝ' ማለት ተቀባይነት ማግኘት ወይም የእርሱ በእርሷ መደሰት የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ በዚህ ስፍራ ዓይን ማየትን የሚያመለክት ስም ሆኖ ጥቅም ላየ ውሏል፣ ማየት ደግሞ የአንድን ነገር ዋጋ መበየንን ወይም መወሰንን ይወክላል፡፡ (ምትክ ስምና ስዕላዊ ንግግርን ተመልከት)

በላችም፣ ፊትዋም

በዚህ ስፍራ ፊትዋ የሚወክለው ራሷን ሐናን ነው፡፡ አስፈላጊ ከሆነ ይህን የተለያየ ዐረፍተ ነገር ማድረግ ትችላለህ፡፡ አት፡- "በላች፡፡ እርሷ ነበረች' ወይም "በላች፡፡ እርሷ እንደ ነበረች ሰዎች ማየት ቻሉ፡፡' (ተለዋጭ ስም ተመልከት)

1 Samuel 1:19

አሰባት

ሐና ይገጥማት የነበረውን ነገር እግዚአብሔር ያውቅ ነበር፣ አልዘነጋትም፡፡ በ1 ሳሙኤል 1፡11 የሚገኙትን ተመሣሣይ ቃላት እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

ሐና ጸነሰች

ሐና አረገዘች

1 Samuel 1:21

ቤቱ

ቤት የሚለው ቃል በቤቱ ውስጥ የሚኖሩ ሰዎችን ለማመልከት ጥቅም ላይ ይውል የነበር ስዕላዊ ስም ነው፡፡ አት፡- "ቤተሰቡ' (ምትክ ስም ተመልከት)

ጡት እስኪተው

ወተት መጠጣት ማቆምና ጠንካራ ምግብ ብቻ መመገብ መጀመር

በእግዚአብሔር ፊት ይታይ ዘንድ፣ በዚያም ለዘላለም ይሆን ዘንድ

ሳሙኤል ከዔሊ ጋር በቤተ መቅደስ እንዲኖርና እንዲያገለግል እንደምታደርግ ሐና ለእግዚአብሔር ቃል ገብታ ነበር (1ሳሙ 1፡11)፡፡

ልጅዋን አጠባች

"ለልጅዋ ወተት ሰጠች'

1 Samuel 1:24

ኢፍ

አንድ ኢፍ 22 ሊትር ደረቀ ነገር ያህል ነው፡፡

ጠርሙስ

ወይን የሚቀመጠው ከእንስሳት ቆዳ በተሰራ እቃ ነው (አቁማዳ)፣ በብርጭቆ ጠርሙስ አልነበረም፡፡

1 Samuel 1:26

ጌታዬ ሆይ በሕያው ነፍስህ እምላለሁ!

በዚህ ስፍራ "በሕያው ነፍስህ' የሚለው ፈሊጣዊ ንግግር ሐና ታማኝና እውነተኛ እንደሆነች ያሳያል፡፡ አት፡- "ጌታዬ ሆይ፣ የምነግርህ ፈጽሞ እውነት ነው፡፡' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

የለመንሁትን ልመናዬን ሰጥቶኛል

"ልመና' የሚለው ስም አንድ ነገር እንዲያደርግ ለሌላ ሰው የቀረበን ይፋ ጥያቄ ያመለክታል፡፡ በማሰሪያ አንቀጽነት ሊተረጎም ይችላል፡፡ "ልመናን መስጠት' የሚለው ፈሊጣዊ ንግግር ሰውዬው የጠየቀውን ማድረግ ማለት ነው፡፡ አት፡- "እንዲያደርግ አጥብቄ የጠየቅሁትን ለማድረግ ተስማማ' (የነገር ስምና ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ለእግዚአብሔር የተሰጠ ይሆናል

በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "ለእግዚአብሔር ሰጥቼዋለሁ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

እግዚአብሔርን አመለከ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) እርሱ የሚለው ሕልቃናን ሊያመለክት ይችላል ወይም 2) እርሱ የሚለው ሁለቱንም ሕልቃናንና ቤተ ሰቡን የሚያመለክት ተለዋጭ ስም ነው፡፡ (ተለዋጭ ስም ተመልከት)


Chapter 2

1 ሐናም እንዲህ በማለት ጸለየች፥ “ልቤ በእግዚአሔር በደስታ ተሞላ። ቀንዴም በእግዚአብሔር ከፍ አለ። በማዳንህ ደስ ብሎኛልና አፌ በጠላቶቼ ላይ ተከፈተ። 2 አንተን የሚመስልህ የለምና፥ እንደ እግዚአብሔር ቅዱስ የለም፤ እንደ አምላካችን ያለም ዐለት የለም። 3 ከእንግዲህ አትታበዩ፤ አንዳች የዕብሪት ንግግር ከአፋችሁ አይውጣ። እግዚአብሔር ዐዋቂ አምላክ ነውና፤ ሥራዎች ሁሉ በእርሱ ይመዘናሉ። 4 የኃያላን ሰዎች ቀስት ተሰብሯል፥ የተሰናከሉት ግን ኃይልን ታጥቀዋል። 5 ጠግበው የነበሩት እንጀራ ለማግኘት ሲሉ ለሥራ ተቀጠሩ፤ ተርበው የነበሩት ረሃብተኝነታቸው አብቅቷል። መካኒቱ እንኳን ሰባት ወልዳለች፥ ብዙ ልጆች የነበሯት ሴት ግን ጠውልጋለች። 6 እግዚአብሔር ይገድላል፥ ያድናልም። ወደ ሲዖል ያወርዳል፥ ያነሣልም። 7 እግዚአብሔር ድሃ ያደርጋል፥ ባለጸጋም ያደርጋል። እርሱ ያዋርዳል፥ ደግሞም ከፍ ያደርጋል። 8 እርሱ ድሃውን ከመሬት ያነሣዋል። ምስኪኖችን ከልዑላን ጋር ሊያስቀምጣቸውና የክብርን ወንበር ሊያወርሳቸው ከአመድ ክምር ላይ ብድግ ያደርጋቸዋል። የምድር መሠረቶች የእግዚአብሔር ናቸውና ዓለምን በእነርሱ ላይ አድርጓል። 9 የታመኑ ሰዎችን እግር ይጠብቃል፥ ማንም በኃይሉ አያሸንፍም፤ ክፉዎች ግን በጨለማ ውስጥ ወዳለው ጸጥታ ይጣላሉ። 10 እግዚአብሔርን የሚቃወሙ ይደቅቃሉ፤ እርሱ ከሰማይ ያንጎደጉድባቸዋል። እግዚአብሔር በምድር ዳርቻዎች ላይ ይፈርዳል፤ የእርሱ ለሆነው ንጉሥ ኃይልን ይሰጠዋል፥ ለቀባውም ቀንዱን ከፍ ያደርግለታል።” 11 ከዚያም ሕልቃና በራማ ወደሚገኘው ቤቱ ሄደ። ልጁም በካህኑ በዔሊ ፊት እግዚአብሔርን ያገለግል ነበር። 12 የዔሊ ወንዶች ልጆች ምንም የማይረቡ ነበሩ። እግዚአብሔርን አያውቁም ነበር። 13 የካህናቱ ልማድ ከሕዝቡ ጋር እንደዚያ ነበርና፥ ማንኛውም ሰው መሥዋዕት ሲያቀርብ፥ ሥጋው እየተቀቀለ እያለ የካህኑ አገልጋይ ሦስት ጣት ያለው ሜንጦ ይዞ ይመጣ ነበር። 14 እርሱም ወደ ድስቱ፥ ወይም ወደ አፍላሉ፥ ወይም ወደ ምንቸቱ ውስጥ ያጠልቀው ነበር። ሜንጦው ያወጣውንም ሁሉ ካህኑ ለራሱ ይወስደው ነበር። ይህንን ወደዚያ ወደ ሴሎ በሚመጡት እስራኤላውያን ሁሉ ላይ ያደርጉ ነበር። 15 ይልቁንም ስቡን ከማቃጠላቸው በፊት የካህኑ አገልጋይ ይመጣና የሚሠዋውን ሰው፥ “ጥሬውን ብቻ እንጂ የተቀቀለውን ሥጋ ከአንተ አይቀበልምና ለካህኑ እንድጠብስለት ሥጋ ስጠኝ" ይለው ነበር። 16 ሰውየው፥ "መጀመሪያ ስቡን ማቃጠል አለባቸው፥ ከዚያም የፈለከውን ያህል መውሰድ ትችላለህ" ካለው ያ ሰው መልሶ፥ "አይደለም፥ አሁኑኑ ስጠኝ፤ እምቢ ካልክም በግድ እወስደዋለሁ" ይለው ነበር። 17 የእግዚአብሔርን መስዋዕት ንቀዋልና የእነዚህ ወጣቶች ኃጢአት በእግዚአብሔር ፊት እጅግ ታላቅ ነበር። 18 ትንሹ ልጅ ሳሙኤል ግን ከተልባ እግር ጨርቅ የተሠራ ኤፉድ ለብሶ እግዚአብሔርን ያገለግል ነበር። 19 እናቱም ዓመታዊውን መሥዋዕት ለማቅረብ ከባሏ ጋር በምትመጣበት ጊዜ በየዓመቱ አነስተኛ መደረቢያ ልብስ እየሠራች ታመጣለት ነበር። 20 ዔሊም ሕልቃናን እና ሚስቱን እንዲህ በማለት ባረካቸው፥”ከእግዚአብሔር በለመነችው ልመና ምክንያት እግዚአብሔር ከዚህች ሴት ተጨማሪ ልጆችን ይስጥህ።“ ከዚያም ወደ ራሳቸው መኖሪያ ተመለሱ። 21 እግዚአብሔር እንደገና ሐናን ረዳት፥ እንደገናም አረገዘች። እርሷም ሦስት ወንዶችና ሁለት ሴት ልጆችን ወለደች። እንዲሁም ትንሹ ልጅ ሳሙኤል በእግዚአብሔር ፊት አደገ። 22 ዔሊ በጣም አርጅቶ ነበር፤ ልጆቹ በእስራኤላውያን ሁሉ ላይ እያደረጉ ያሉትን በሙሉ እና በመገናኛው ድንኳን መግቢያ ከሚያገለግሉት ሴቶች ጋር እንደ ተኙ ሰማ። 23 እርሱም እንዲህ አላቸው፥”ስለ ክፉ ሥራችሁ ከዚህ ሕዝብ ሁሉ ሰምቻለሁና እንደዚህ ያሉትን ነገሮች የምትፈጽሙት ለምንድነው? 24 ልጆቼ ሆይ፥ የምሰማው መልካም ወሬ አይደለምና ልክ አይደላችሁም። የእግዚአብሔር ሕዝብ እንዲያምጽ ታደርጉታላችሁ። 25 አንድ ሰው ሌላውን ቢበድል፥ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ ይፈርዳል፤ አንድ ሰው ግን በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአትን ቢሠራ ስለ እርሱ የሚናገር ማን ነው?" እነርሱ ግን እግዚአሔር ሊገድላቸው ፈልጓልና የአባታቸውን ቃል አልሰሙም። 26 ትንሹም ልጅ ሳሙኤል አደገ፥ በእግዚአብሔርና በሰዎችም ፊት ደግሞ በሞገስ እያደገ ሄደ። 27 አንድ የእግዚአብሔር ሰው ወደ ዔሊ መጥቶ እንዲህ አለው፥ “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ 'በግብፅ አገር፥ በፈርዖን ቤት ባሪያዎች በነበሩ ጊዜ ለአባትህ ቤት ራሴን ገለጥኩኝ፤ 28 ከእስራኤል ነገዶች ሁሉ ካህን እንዲሆነኝ፥ ወደ መሠዊያዬ እንዲወጣ፥ ዕጣን እንዲያጥንልኝ፥ በፊቴም ኤፉድ እንዲለብስ መረጥኩት። የእስራኤል ሕዝብ በእሳት የሚያቀርበውን መባ ሁሉ ለአባትህ ቤት ሰጠሁ። 29 ታዲያ በማደሪያዬ ያዘዝኩትን መሥዋዕትና መባ የምትንቁት ለምንድነው? በሕዝቤ በእስራኤል ከሚቀርበው መስዋዕት ሁሉ በተመረጠው እየወፈራችሁ ልጆችህን ከእኔ በላይ ያከበርከው ለምንድነው?' 30 የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ 'ቤትህና የአባትህ ቤት ለዘላለም በፊቴ እንዲመላለስ ተስፋ ሰጥቼ ነበር'። አሁን ግን እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ 'ይህንን ማድረግ ከእኔ ይራቅ፥ የሚያከብሩኝን አከብራለሁና የሚንቁኝ ግን ፈጽሞ ይናቃሉ። 31 ተመልከት፥ ከእንግዲህ በቤትህ ሽማግሌ የሚሆን አንድም ሰው እንዳይኖር ያንተን ኃይልና የአባትህን ቤት ኃይል የምቆርጥበት ቀን ቀርቧል። 32 በማድርበት ስፍራም መከራን ታያለህ። ለእስራኤል መልካም ነገር ቢሰጥም ከእንግዲህ በቤትህ ሽማግሌ የሚሆን አንድ ሰው አይኖርም። 33 ያንተ የሆኑትና ከመሠዊያዬ የማልቆርጣቸው ማናቸውም ዐይኖችህን እንዲያፈዝዙና ሕይወትህን በሐዘን እንዲሞሉት አደርጋቸዋለሁ። በቤተ ሰብህ ውስጥ የተወለዱ ወንዶች ሁሉ ይሞታሉ። 34 በሁለቱ ወንዶች ልጆችህ በአፍኒን እና በፊንሐስ የሚደርስባቸው ምልክት ይሆንሃል፤ ሁለቱም በአንድ ቀን ይሞታሉ። 35 በልቤና በነፍሴ ውስጥ ያለውን የሚፈጽም ታማኝ ካህን ለራሴ አስነሣለሁ። የማያጠራጥር ቤት እሠራለታለሁ፤ ለዘላለምም በቀባሁት ንጉሥ ፊት ይሄዳል። 36 ከቤተ ሰብህ የተረፈ ሁሉ ጥቂት ጥሬ ብርና ቁራሽ እንጀራ እንዲሰጠው ለመለመን በዚያ ሰው ፊት መጥቶ ይሰግዳል፥ 'ቁራሽ እንጀራ መብላት እንድችል እባክህ ከካህናቱ ኃላፊነቶች በአንዱ ስፍራ መድበኝ'" ይለዋል።



1 Samuel 2:1

አጠቃላይ መረጃ

ሐና ለእግዚአብሔር መዝሙር ዘመረች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

ልቤ ፈነደቀ

"ታላቅ ደስታ አለኝ'

በእግዚአብሔር

"ከእግዚአብሔር ማንነት የተነሣ' ወይም "እግዚአብሔር እጅግ ታላቅ ከመሆኑ የተነሣ'

ቀንዴ ከፍ ከፍ አለ

ቀንድ የብርታት ምልክት ነው፡፡ አት፡- "አሁን ብርቱ ነኝ' (ዘይቤአዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 2:2

አያያዥ አሳብ

ሐና ለእግዚአብሔር መዘመሯን ቀጥላለች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

እንደ አምላካችን ያለ ዓለት የለም

ይህ እግዚአብሔር ብርቱና የታመነ ነው የሚለው ሌላኛው አባባል ነው፡፡ (ዘይቤአዊ አነጋገር ተመልከት)

ዓለት

ይህ ዓለት ከበስተኋላው ለመደበቅ ወይም በላዩ ላይ ለመቆም እና አንድ ሰው ከጠላቶቹ በላይ እጅግ ከፍ ለማለት በቂ የሆነ ዓለት ነው፡፡

1 Samuel 2:3

አያያዥ አሳብ

ሐና ለእግዚአብሔር መዘመሯን ቀጥላለች፡፡ ሌሎች ሰዎች እየሰሟት እንዳሉ አድርጋ ትናገራለች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

አትታበዩ

"በትዕቢት አትናገሩ'

ሥራዎች በእርሱ ይመዘናሉ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት እርሱ የሰዎችን ሥራዎች ይመዝናል ወይም ሰዎች የሚያደርጉትን ለምን እንደሚያደርጉ ያውቃል (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

የኃያላን ሰዎች ቀስት ተሰብሮአል

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡፡ 1) ቀስቶቹ ራሳቸው ተሰብረዋል ወይም 2) ቀስት የያዙ ሰዎች ከማድረግ ተከለከሉ፡፡ አት፡- "ኃያላን ቀስተኞች ሰዎች ከማድረግ ተከለከሉ'

የኃያላን ሰዎች ቀስት ተሰብሮአል

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር የኃያላን ሰዎችን ቀስት ይሰብራል' ወይም "እግዚአብሔር ኃያላን ሰዎችን እንኳን ደካሞች ያደርጋል' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

ደካሞች (የሚሰናከሉ) እንደ መታጠቂያ ኃይልን ታጥቀዋል

ይህ ዘይቤአዊ ንግግር ከእንግዲህ ወዲህ አይሰናከሉም ነገር ግን ኃይላቸው እንደ መታጠቂያ ጠብቆ አብሯቸው ይኖራል ማለት ነው፡፡ አት፡- "የሚሰናከሉትን ብርቱዎች ያደርጋቸዋል' (˜ይቤአዊ ንግግር ተመልከት)

መታጠቂያ … ታጥቀዋል

ይህ ለሥራ ለመዘጋጀት አንድን ነገር በወገብ ዙሪያ ስለማሰረ ጥቅም ላይ የሚውል አጠቃላይ ቃል ነው፡፡

1 Samuel 2:5

አያያዥ አሳብ

ሐና ለእግዚአብሔር መዘመሯን ቀጥላለች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

ሰባት ወልዳለች

"ሰባት ልጆች ወልዳለች'

ደክማለች

ደካማ፣ ሐዘንተኛና ብቸኛ መሆን

1 Samuel 2:6

አያያዥ አሳብ

ሐና ለእግዚአብሔር መዘመሯን ቀጥላለች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

እግዚአብሔር ይገድላል፣ ያድናል … ያወርዳል፣ያወጣል … ድሀ ያደርጋል፣ ባለጠጋም ያደርጋል፣ ያዋርዳል፣ ከፍ ከፍ ያደርጋል

እግዚአብሔር ሁሉን ይቆጣጠራል፡፡ (ስዕላዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 2:8

አያያዥ አሳብ

ሐና ለእግዚአብሔር መዘመሯን ቀጥላለች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

ከመሬት … ከጉድፍ

በማኅበረ ሰቡ ውስጥ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ለሚገኙ ጥቅም ላይ የሚውል ዘይቤአዊ ንግግር ነው፡፡ (ዘይቤአዊ ንግግር ተመልከት)

ችግረኞች

የሚያስፈልጓቸው ነገሮች የሌሏቸው፡፡

1 Samuel 2:9

አያያዥ አሳብ

ሐና ለእግዚአብሔር መዘመሯን ቀጥላለች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

የታማኞቹን ሰዎች እግር ይጠብቃል

በዚህ ስፍራ "እግር' የሚለው ስም አንድ ሰው ለሚሄድበት መንገድ ጥቅም ላይ የሚውል ስዕላዊ ንግግር ነው፣ በሌላ በኩል ደግሞ አንድ ሰው ሕይወቱን ለመኖር የወሰነበትን መንገድ የሚያመለክት ዘይቤአዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "የተሳሳተ ውሳኔ እንዳይወስኑ ታማኞቹን ይጠብቃል' ወይም "ታማኞቹን ሰዎች ተገቢ ውሳኔ እንዲወስኑ ያስችላቸዋል፡፡' (ስዕላዊና ዘይቤአዊ ንግግር ተመልከት)

ኃጢአን ግን ዝም ብለው በጨለማ ይቀመጣሉ

በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ እግዚአብሔር ኃጢአተኛውን ይገድላል በሚል ሊገለጽ የሚችለው የተነገረበት የአክብሮት መንገድ ነው፡፡ አት "እግዚአብሔር ኃጢአተኛውን በጨለማ ዝምታ ውስጥ ያስቀምጣል' ወይም "እግዚአብሔር ኃጢአተኛውን በጨለማና በሙታን የዝምታ ዓለም ውስጥ ያስቀምጣል' (የማያስደስትን ቃል በሌላ ቃል መጠቀም ተመልከት)

ኃጢአን በዝምታ እንዲቀመጡ ይደረጋሉ

"በዝምታ እንዲቀመጡ ይደረጋሉ' የሚሉት ቃላት "ዝም እንዲሉ ይደረጋሉ' ለሚለው ፈሊጣዊ ንግግር ናቸው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር እና አድራጊና ተደረጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

በኃይሉ

"ኃይለኛ ከመሆኑ የተነሳ'

1 Samuel 2:10

አያያዥ አሳብ

ሐና ለእግዚአብሔር መዘመሯን ቀጥላለች፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

እግዚአብሔርን የሚቃወሙ ይደቅቃሉ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር እርሱን የሚቃወሙትን ያደቅቃቸዋል፡፡' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

ያደቅቃቸዋል

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር "ያሸንፋቸዋል' ማለት ነው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

እስከ ምድር ዳርቻ

በሁሉ ስፍራ የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "ምድር ሁሉ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

የመሲሑን ቀንድ ከፍ ከፍ ያደርጋል

ቀንድ የጥንካሬ ምልክት ነው፡፡ ተመሣሣይ ቃላትን በ1ሳሙኤል 2፡1 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ አት፡- "የመረጠውን መሪ ከጠላቶቹ በላይ ብርቱ ያደርገዋል' (ዘይቤአዊ ንግግር ተመልከት)

መሲሑ

ይህ እግዘአብሔር ሰውዬውን በዘይት እንደቀባው አድርጎ የሚናገረው እግዚብሔር ለዓላማው ስለ መረጠውና ሥልጣን ስለ ሰጠው ነው፡፡ አት፡- "የቀባው' ወይም "የመረጠው' (ዘይቤአዊ ንግግርና አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽን ተመልከት)

1 Samuel 2:12

አጠቃላይ መረጃ

ሰዎች እንስሳትን በመሥዋዕትነት ሲያቀርቡ በመጀመሪያ የእንስሳውን ስብ ማቃጠል፣ ሥጋውን መቀቀልና መብላት አለባቸው፡፡

እግዚአብሔርን አያውቁም ነበር

"እግዚአብሔርን አይሰሙም ነበር' ወይም "እግዚአብሔርን አይታዘዙም ነበር'

ልማድ

ልማድ ሰዎች በቋሚነት የሚያከናውኑት ተግባር ነው፡፡

ወደ ድስቱ … ወይም ምንቸቱ … ወይም አፍላሉ … ወይም ቶፋው

እነዚህ ምግብ የሚበስልባቸው ዕቃዎች ናቸው፡፡ ቋንቋህ ለእነዚህ ዕቃዎች የተለያዩ ቃላት ከሌለው በአጠቃላይ መልኩ ሊገለጹ ይችላላል፡፡አት፡- "በማናቸውም ሰዎች ሥጋ በሚያበስሉባቸው ውስጥ'

ድስት

ከሸክላ የተሠራ ማብሰያ

ምንቸት

የሸክላ ድስት

አፍላላ

ተለቅ ያለ ማብሰያ ድስት

ቶፋው

አነስተኛ ማብረጃ

1 Samuel 2:15

አጠቃላይ መረጃ

ሰዎች እንስሳትን በመሥዋዕትነት ሲያቀርቡ በመጀመሪያ የእንስሳውን ስብ ማቃጠል፣ ሥጋውን መቀቀልና መብላት አለባቸው፡፡

የባሰ፣ በፊት

"ከዚያም እንኳን የባሰ ያደርጉ ነበር፡፡ በፊት'

ያቃጥሉት

በተጨባጭ የሚያቃጥለውን ሰው ግልጽ ማድረግ ይቻላል፡፡ አት፡- "መሥዋዕት ያቀርብ የነበረው ሰው መስዋዕቱን ወደ ካህናቱ ያመጣዋል፣ ካህናቱም ያቃጥሉታል፡፡' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትንና ያልተገለጸ መረጃን ተመልከት)

እጠብስለት ዘንድ ለካህኑ ሥጋ ስጠኝ

"እንዲጠብሰው ለካህኑ እሰጠው ዘንድ ሥጋ ስጠኝ'

መጥበስ

እሳት ላይ ማብሰል

መቀቀል

በፈላ ውኃ ማብሰል

ጥሬ

ያልበሰለ

የእግዚአብሔርን ቁርባን ይንቁ ነበር

እግዚአብሔር ቁርባንን በሚመለከት የሰጠውን መመሪያ ወጣቶቹ አይወዱም ትኩረትም አይሰጡትም ነበር፡፡

1 Samuel 2:20

ለእግዚአብሔር ካቀረበችው ልመና የተነሣ

ሐና እግዚአብሔር ልጅ እንዲሰጣት ለመነችው፣ በመቅደስም እንዲያገልገል ልጁን ለመስጠት ቃል ገባች፡፡

በእግዚአብሔር ፊት

ይህም እግዚአብሔር እርሱን በሚያይበትና ሳሙኤል ስለ እግዚአብሔር ሊማር በሚችልበት ቦታ ማለት ነው፡፡

1 Samuel 2:22

ስለ ምን እንዲህ ያለ ነገር ታድርጋላችሁ?

ይህ አሳብ ገላጭ ጥያቄ በገላጭ አባባል ይችላል፡፡ አት፡- "እንዲህ ዓይነት ነገር ማድረጋችሁ በጣም አሳዛኝ ነው፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

1 Samuel 2:25

ስለ እርሱ የሚናገር ማን ነው?

ይህ አሳብ ገላጭ ጥያቄ በገላጭ አባባል ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "በእርግጥ ስለ እርሱ የሚናገር ማንም የለም፡፡'(አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ስለ እርሱ የሚናገር

"ምሕረት እንዲያደርገለት እግዚአብሔርን የሚለምንለት'

የአባታቸው ድምጽ

በዚህ ስፍራ የአባት ድምጽ አባታን ይወክላል፡፡ አት፡- "አባታቸው' ወይም "አባታቸው ያላቸውን' (ተለዋጭ ስም ተመልከት)

1 Samuel 2:27

የእግዚአብሔር ሰው

ብዙ ጊዜ ይህ ሃረግ የእግዚአብሔር ነቢይ ማለት ነው፡፡ አት "ከእግዚአብሔር ቃላት የሚሰማና የሚናገር ሰው'

ቤት … ራሴን አልገለጥሁምን

ይህ አሳብ ገላጭ ጥያቄ እንደሚከተለው ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት "ቤት … ራሴን እንደገለጥሁ ልታውቅ ይገባሃል፡፡'

ለአባትህ ቤት

"ቤት' የሚለው ስም በቤቱ ውስጥ ላሉ ሰዎች ምትክ ስም ነው፡፡ አት ፡- "የአባትህ ቤተሰብ' (ምትክ ስም ተመልከት)

አባትህ

አሮን

ወደ መሠዊያዬ ይወጣ ዕጣንም ያጥን ዘንድ

ይህ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት ማቅረብን ያመለክታል፡፡

ኤፉድንም በፊቴ ይለብስ ዘንድ

"ኤፉድ መልበስ' የሚሉት ቃላት ኤፉድ ለሚለብሱት ካህናት ሥራ ምትክ ስም ነው፡፡ አት፡- "ካህናት ያደርጉ ዘንድ ያዘዝኩትን ያደርግ ዘንድ፡፡' (ምትክ ስም ተመልከት)

1 Samuel 2:29

አያያዥ አሳብ

የእግዚአብሔር ሰው ለዔል መናገሩን ቀጠለ

በማደሪያዬ … መሥዋዕቴን ስለምን ናቃችሁ?

ይህ አሳብ ገላጭ ጥያቄ የሚገሥጽ ነው፡፡ በገላጭ አባባልነት ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት "በማደሪያዬ … መሥዋዕቴን ልትንቁ አይገባችሁም፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ማደሪያዬን

"ሕዝቤ ቁርባን ለእኔ የሚያቀርቡበት ቦታ'

ከእያንዳንዱ ቁርባን በተሻለው ራሳችሁን ለማወፈር

ከቁርባኑ የተሻለው ክፍል ለእግዚአብሔር ቁርባን ሆኖ መቃጠል ነበረበት፣ ካህናቱ ግን፡ ይበሉት ነበር፡፡

የአባትህ ቤት

"ቤት' የሚለው ስም በቤቱ ውስጥ ላሉ ሰዎች ምትክ ስም ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 2፡27 እንዴት እንደተረጎምከው ተመልከት፡፡ አት ፡- "የአባትህ ቤተሰብ' (ምትክ ስም ተመልከት)

በፊቴ ልትሄድ ይገባሃል

ይህ "ለእኔ በመታዘዝ ኑር' የሚል ትርጉም ያለው ዘይቤአዊ አነጋገር ነው፡፡ (ዘይቤአዊ አነጋገር ተመልከት)

ይህን ማድረግ ከእኔ ይራቅ

"በእርግጥ ቤተሰብህ እኔን ለዘላለም እንዲያገለግለኝ አልፈቅድም'

የናቁኝ በጥቂቱ ይከብራሉ

"በጥቂቱ ይከበራሉ' የሚሉት ቃላት "እጅግ ይዋረዳሉ' ለሚለው የማያስደስት ቃል በምጸት የተተካ ቃል ነው፡፡ ይህ በአድራጊ አንቀጽ እንደሚከተለው ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "የሚንቁኝን በጥቂቱ አከብራለሁ' ወይም "የሚንቁኝን በእጅጉ አዋርዳለሁ' (ምጸት፣የማያስደስትን ቃል በሌላ ቃል መጠቀም እና አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

1 Samuel 2:31

እይ

"የምናገረውን በጥንቃቄ አድምጥ' ወይም "የምናገረው ነገር በጣም አስፈላጊ ነው'

የአንተንና የአባትህን ቤት ብርታት እቆርጣለሁ

"… ብርታት እቆርጣለሁ' የሚለው የብርቱዎችንና የወጣቶችን ሞት በማይከብድ ቃል ለመተካት ጥቅም ላይ የዋለ ሳይሆን አይቀርም፡፡ "የአባትህ ቤት' የሚሉት ቃላት "ቤተሰብህ' ለሚለው ምትክ ናቸው፡፡ (የማያስደስትን ቃል በሌላ ቃል መጠቀም እና ምትክ ቃል ተመልከት)

ማንኛውም ሽማግሌ ቢሆን

"ማንኛውም ሽማግሌ ቢሆን' ወይም "ያረጀ ማንኛውም ሰው ቢሆን'

ዓይኖችህ እንዳይሠሩ ያደርጋል

"እይታህን እንድታጣ ያደርጋል' ወይም "ዓይነ ስውር እንድትሆን ያደርጋል'

1 Samuel 2:34

የታመነ ካህን አስነሳለሁ

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "አንድ ሰው ካህን አደርጋለሁ፡፡' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ለራሴ (ለእኔ)

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "እንዲያገለግለኝ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

በልቤና በነፍሴ ያለውን

"እንዲያደርግ የምፈልገውንና እንዲያደርግ የምነግረውን'

የታመነ ቤት እሠራለታለሁ

በዚህ ስፍራ "ቤት' የሚለው "ትውልድን' የሚመለክት ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "ሁሌም ሊቀ ካህን ሆኖ የሚያገለግል ትውልድ እንደሚኖረው ቃል እገባለሁ፡፡'(ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 2:36

እርሱ

እግዚአብሔር የሚያስነሳው የታመነ ካህን

ቁራሽ እንጀራ እበላ ዘንድ

በዚህ ስፍራ "ቁራሽ እንጀራ' የሚለው "ምግብን' ለማመልከት ጥቅም ላይ የዋለ ነው፡፡ አት፡- "አንዳች የምበላው ነገር እንዲኖረኝ' (ተለዋጭ ስም ተመልከት)


Chapter 3

1 ትንሹ ልጅ ሳሙኤል በዔሊ ሥር ሆኖ እግዚአብሔርን ያገለግል ነበር። 2 በእነዚያ ቀናት የእግዚአብሔር ቃል እምብዛም አይገኝም ነበር፤ ትንቢታዊ ራዕይም አይዘወተርም ነበር። በዚያን ጊዜ፥ ዔሊ ዐይኖቹ ከመፍዘዛቸው የተነሣ አጥርቶ ማየት ባቃተው ጊዜ፥ በአልጋው ላይ ተኝቶ እያለ፥ 3 የእግዚአብሔር መብራት ገና አልጠፋም ነበር፥ ሳሙኤል የእግዚአብሔር ታቦት ባለበት በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ተኝቶ ነበር። 4 እግዚአብሔር ሳሙኤልን ጠራው፥ እርሱም፥ “አቤት!” አለው። 5 ሳሙኤል ወደ ዔሊ ሮጠና፥ “ጠርተኸኛልና ይኸው መጥቻለሁ” አለው፤ ዔሊም፥ “እኔ አልጠራሁህም፤ ተመልሰህ ተኛ” አለው። ስለዚህ ሳሙኤል ሄደና ተኛ። 6 እግዚአብሔር እንደገና፥ “ሳሙኤል” ብሎ ተጣራ። ሳሙኤልም እንደገና ተነሥቶ ወደ ዔሊ ሄደና፥ “ጠርተኸኛልና ይኸው መጥቻለሁ” አለው። ዔሊም፥ "ልጄ ሆይ፥ እኔ አልጠራሁህም፤ ተመልሰህ ተኛ" ብሎ መለሰለት። 7 ሳሙኤል እግዚአብሔርን ገና አላወቀም ነበር፥ ከእግዚአብሔር ምንም ዓይነት መልዕክት ገና አልተገለጠለትም ነበር። 8 እግዚአብሔር ሳሙኤልን እንደገና ለሦስተኛ ጊዜ ጠራው። ሳሙኤልም እንደገና ተነሥቶ ወደ ዔሊ ሄደና፥ “ጠርተኸኛልና ይኸው መጥቻለሁ” አለው። ከዚያም ልጁን እግዚአብሔር እንደ ጠራው ዔሊ አስተዋለ። 9 ዔሊም ሳሙኤልን፥ "ሂድና ተመልሰህ ተኛ፤ ደግሞ ከጠራህም፥ 'እግዚአብሔር ሆይ፥ አገልጋይህ እየሰማህ ነውና ተናገር' ማለት አለብህ" አለው። ስለዚህ ሳሙኤል እንደገና ወደ ስፍራው ተመልሶ ተኛ። 10 እግዚአብሔርም መጥቶ ቆመ፤ እንደ ቀድሞው ሁሉ፥ "ሳሙኤል፥ ሳሙኤል" ብሎ ጠራው። ከዚያም ሳሙኤል፥ "አገልጋይህ እየሰማህ ነውና ተናገር" አለው። 11 እግዚአብሔርም ሳሙኤልን እንዲህ አለው፥ "ተመልከት፥ የሚሰማውን ሁሉ ጆሮውን ጭው የሚያደርግ አንድ ነገር በእስራኤል ላይ አደርጋለሁ። 12 በዚያም ቀን፥ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ስለ ቤቱ የተናገርኩትን ሁሉ በዔሊ ላይ አመጣበታለሁ። 13 ልጆቹ በራሳቸው ላይ እርግማንን ስላመጡና እርሱም ስላልከለከላቸው፥ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እርሱ ስለሚያውቀው ኃጢአት በቤቱ ላይ እንደምፈርድ ነግሬዋለሁ። 14 በዚህ ምክንያት የቤቱ ኃጢአት በመሥዋዕት ወይም በመባ ይቅር እንዳይባል ለዔሊ ቤት ምያለሁ።" 15 ሳሙኤል እስኪነጋ ተኛ፤ ከዚያም የእግዚአብሔርን ቤት በሮች ከፈተ። ሳሙኤል ግን ስላየው ራዕይ ለዔሊ ለመንገር ፈራ። 16 ከዚያም ዔሊ ሳሙኤልን ጠርቶ፥ "ልጄ ሳሙኤል ሆይ" አለው። ሳሙኤልም፥ "አቤት!" ብሎ መለሰለት። 17 እርሱም፥ "የነገረህ ቃል ምንድነው? እባክህ አትደብቀኝ። ከነገረህ ቃል ሁሉ አንዱን ብትደብቀኝ እግዚአብሔር ይህን ያድርግብህ፤ ከዚያም የባሰውን ጨምሮ ያድርግብህ" አለው። 18 ሳሙኤል ሁሉንም ነገር ነገረው፤ ከእርሱም ምንም አልደበቀም። ዔሊም፥ "እርሱ እግዚአብሔር ነው። መልካም መስሎ የታየውን ያድርግ" አለ። 19 ሳሙኤል አደገ፥ እግዚአብሔርም ከእርሱ ጋር ነበር፥ ከትንቢታዊ ቃሉ ሳይፈጸም የቀረ አንድም አልነበረም። 20 ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ያሉት እስራኤላውያን በሙሉ ሳሙኤል የእግዚአብሔር ነቢይ እንዲሆን መመረጡን ዐወቁ። 21 እግዚአብሔር እንደገና በሴሎ ተገለጠ፥ እርሱም በቃሉ አማካይነት በሴሎ ራሱን ለሳሙኤል ገለጠለት።



1 Samuel 3:1

የእግዚአብሔር ቃል ብርቅ ነበር

እግዚአብሔር ብዙ ጊዜ ለሕዝብ አይናገርም ነበር

የእግዚአብሔር መብራት

ይህ በመገናኛው ድንኳን ቅዱስ ስፍራ በሁሉም ቀን እና ባዶ እስኪሆን ድረስ ሌሊቱን ሁሉ የሚነደው ሰባት መቅረዝ ያለው መብራት ነው፡፡

የእግዚአብሔር መቅደስ

"መቅደሱ' በእርግጥ ድነኳን ነበር ነገር ግን ሕዝቡ ያመልክበት የነበረ ስፍራ ስለ ነበር፣ በዚህ ስፍራ መቅደስ ብሎ መተረጎም ይበልጥ የተመረጠ ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 1፡9 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

1 Samuel 3:5

ልጄ

ዔሊ የሳሙኤል እውነተኛ አባት አልነበረም፡፡ ዔሊ የሳሙኤል አባት እንደሆነ አድርጎ መናገሩ እንዳልተበሳጨ ነገር ግን ሳሙኤል ሊሰማው እንደሚገባ ለሳሙኤል ለማሳየት ነው፡፡ (ዘይቤአዊ አነጋገር ተመልከት)

1 Samuel 3:7

ምንም መልእክት ከእግዚአብሔር ዘንድ ገና አልተገለጠለትም ነበር

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር ምንም መልእከት መቼም አልገለጠለትም ነበር' ወይም "እግዚአብሔር ምንም መልእክት ፈጽሞ አልገለጠለትም ነበር፡፡' (አድጊራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመለከት)

1 Samuel 3:9

አገልጋይህ

ሳሙኤል ለእግዚአብሔር አክበሮትን ለማሳየት ራሱን እንደ ሌላ ሰው አድርጎ ሳሙኤል ለእግዚአብሔር እንዲናገር ዔሊ ነገረው፡፡ አት፡- 'እኔ ነኝ' (ተውላጠ ስም ተመልከት)

1 Samuel 3:10

እግዚአብሔርም መጥቶ ቆመ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1)እግዚአብሔር በተጨባጭ ተገልጦአል በሳሙኤልም ፊት ቆሞአል 2)እግዚአብሔር መገኘቱን ለሳሙኤል እንዲታወቅ አድርጓል

አገልጋይህ

ሳሙኤል ለእግዚአብሔር አክበሮትን ለማሳየት ራሱን እንደ ሌላ ሰው አድርጎ ለእግዚአብሔር ተናገረ፡፡ አት፡- 'እኔ ነኝ' (ተውላጠ ስም ተመልከት)

የሰማውን ሁሉ ጆሮች ጭው የሚያደርግ

በዚህ ስፍራ "ጆሮች ጭው የሚያደርግ' የሚለው ስለ ሰሙት ነገር እያንዳንዳቸው ይደነግጣሉ የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "የሚሰማውን እያንዳንዱን ያስደነግጣል' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ጭው

በተለምዶ ከቅዝቃዜ የተነሳ ወይም ያንን የሰወነት ክፍል ሰዎች በእጃቸው ከመምታቸው የተነሳ አንድ ሰው በትንሽ የተሳለ ነገር በቀላሉ ሲወጋ የሚሰማው የመወጋት ስሜት ዓይነት ነው፡፡

1 Samuel 3:12

ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ

ይህ ሙሉነትን የሚያሳይ ስዕላዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "ፈጽሞ ሁሉን ነገር' (ስዕላዊ ንግግር ተመልከት)

መርገምን በራሳቸው ላይ አመጡ

"የሚያደርጓቸውን እነዚያን ሰዎች እቀጣለሁ ብሎ እግዚአብሔር የተናገረባቸውን እነዚያን ነገሮች አደረጉ'

የዔሊ ቤት ኃጢአት በመሥዋዕትና በቁርባን ፈጽሞ አይሰረይም

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "የቤቱን ኃጢአት ሊያስተሰርይ የሚችል ማንም ሊያቀርበው የሚችል መስዋዕት ወይም ቁርባን የለም' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

የዔሊ ቤት ኃጢአት

በቤተሰቡ ውስጥ የሚገኙ ሰዎች የፈጸሙት ኃጢአት ነው

1 Samuel 3:15

የእግዚአብሔር ቤት

"ቤት' የተባለው በተጨባጭ "ድንኳን' ነበር፣ ነገር ግን በዚህ ስፍራ "ቤት' ብሎ መተርጎሙ እጅግ የተሻለ ነው፡፡

ልጄ

ዔሊ የሳሙኤል እውነተኛ አባት አልነበረም፡፡ ዔሊ የሳሙኤል አባት እንደሆነ አድርጎ መናገሩ እንዳልተበሳጨ ነገር ግን ሳሙኤል ሊመልስለት እንደሚገባ ለሳሙኤል ለማሳየት ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 3፡6 እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት፡፡ (ዘይቤአዊ አነጋገር ተመልከት)

1 Samuel 3:17

የተናገረውን ቃል

"እግዚአብሔር የሰጠው መልእክት'

እግዚአብሔር እንዲህ ያድርግብህ እንዲህም ይጨምርብህ

ይህ ዔሊ ምን ያህል የምሩን እንደሆነ አጽንዖት የሚሰጥ ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር እኔን እንደሚቀጣ በተናገረበት ተመሳሳይ መንገድ ይቅጣህ፣ ከዚያም በላይ እንኳን ይጨምርብህ፡፡' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 3:19

ከቃሉም አንዳች በምድር ላይ አይወድቅም ነበር

በዚህ ስፍራ ያልተፈጸሙ መልእክቶች መሬት ላይ እንደወደቁ ተገልጸዋል፡፡ ይህ አዎንታዊ በሆነ መልኩ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "የተነበያቸው ነገሮች ሁሉ ይፈጸሙ ነበር' (ዘይቤአዊ ንግግርና ሁኔታን በማንበብ ላይ የተመሠረተ ትንቢት ተመልከት)

እስራኤል ሁሉ

"በእስራኤል ያሉ ሰዎች ሁሉ'

ከዳን እስከ ቤርሳቤህ

"በምድሪቱ ክፍል ሁሉ' የሚልን አሳብ የሚያመለክት ስዕላዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "ከምድሪቱ አንደኛው ጫፍ እስከ ሌላኛው ጫፍ' ወይም "ከሰሜን ጥግ ከዳን እስከ ደቡብ ጥግ እስከ ቤርሳብህ'

ሳሙኤል ተሾመ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይቻላል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር ሳሙኤልን ሾመ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)


Chapter 4

1 የሳሙኤልም ቃል ወደ እስራኤላውያን ሁሉ መጣ። በዚህ ወቅት እስራኤላውያን ከፍልስጥኤማውያን ጋር ለመዋጋት ሄዱ። የጦር ሰፈራቸውንም በአቤንኤዘር አደረጉ፥ ፍልስጥኤማውያንም የጦር ሰፈራቸውን በአፌቅ አደረጉ። 2 ፍልስጥኤማውያንም ከእስራኤላውያን ጋር ለመዋጋት ተሰለፉ። ውጊያው በተፋፋመ ጊዜ እስራኤላውያን አራት ሺህ ሰዎቻቸው በውጊያው ሜዳ በመገደላቸው በፍልስጥኤማውያን ተሸነፉ። 3 ሕዝቡ ወደ ጦር ሰፈሩ በመጣ ጊዜ፥ የእስራኤል ሽማግሌዎች፥ "እግዚአብሔር ዛሬ በፍልስጥኤማውያን ፊት እንድንሸነፍ ያደርገን ለምንድነው? ከእኛ ጋር እንዲሆንና ከጠላቶቻችን ኃይል እንዲያድነን የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት ከሴሎ እናምጣው" አሉ። 4 ስለዚህ ሕዝቡ ወደ ሴሎ ሰዎችን ላኩ። ከዚያ በኪሩቤል ላይ የሚቀመጠውን የሠራዊቱን ጌታ የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት አመጡ። ሁለቱ የዔሊ ልጆች አፍኒንና ፊንሐስ ከእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ታቦት ጋር በዚያ ነበሩ። 5 የእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ታቦት ወደ ጦር ሰፈሩ በመጣ ጊዜ፥ የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ በታላቅ ዕልልታ ጮኹ፥ ምድሪቱም አስተጋባች። 6 ፍልስጥኤማውያን የዕልልታውን ድምፅ በሰሙ ጊዜ፥ “ይህ በዕብራውያኑ የጦር ሰፈር የሚሰማው የዕልልታ ድምፅ ምን ማለት ይሆን? አሉ። ከዚያም የእግዚአብሔር ታቦት ወደ ጦር ሰፈሩ እንደ መጣ ተገነዘቡ። 7 ፍልስጥኤማውያኑ ፈሩ፤ እነርሱም፥”እግዚአብሔር ወደ ጦር ሰፈሩ መጥቷል" አሉ። 8 እነርሱም፥ "ወዮልን! እንደዚህ ያለ ነገር ከአሁን በፊት አልሆነም! ወዮልን! ከዚህ ኃያል አምላክ ክንድ ማን ያድነናል? ይህ በምድረ በዳ ግብፃውያንን በልዩ ልዩ ዓይነት መቅሠፍት የመታቸው አምላክ ነው። 9 እናንተ ፍልስጥኤማውያን በርቱ፥ ወንድነታችሁንም አሳዩ፥ ካልሆነ እነርሱ ባሪያዎቻችሁ እንደነበሩ ባሪያዎቻቸው ትሆናላችሁ። ወንድነታችሁ ይታይ፥ ተዋጉም" አሏቸው። 10 ፍልስጥኤማውያኑ ተዋጉ፥ እስራኤላውያንም ተሸነፉ። እያንዳንዱ ወደ ቤቱ ሸሸ፥ የተገደሉትም እጅግ ብዙ ነበሩ፤ ከእስራኤል ሠላሳ ሺህ እግረኛ ወታደር ወደቀ። 11 የእግዚአብሔር ታቦት ተወሰደ፥ ሁለቱ የዔሊ ልጆች አፍኒንና ፊንሐስም ሞቱ። 12 በዚያው ቀን አንድ ብንያማዊ ከውጊያው መስመር ወደ ሴሎ በሩጫ መጣ፥ በደረሰ ጊዜ ልብሱን ቀድዶና በራሱ ላይ አፈር ነስንሶ ነበር። 13 እርሱ በደረሰ ጊዜ፥ ዔሊ ስለ እግዚአብሔር ታቦት በመስጋት ልቡ ታውኮበት ስለነበረ በመንገዱ ዳር ወንበሩ ላይ ተቀምጦ ነበር። ሰውየው ወደ ከተማ ገብቶ ወሬውን በነገራቸው ጊዜ፥ ከተማው በሙሉ አለቀሱ። 14 ዔሊ የልቅሶውን ድምፅ በሰማ ጊዜ፥ “የዚህ ሁካታ ትርጉሙ ምንድነው?” አለ። ሰውየው ፈጥኖ መጣና ለዔሊ ነገረው። 15 በዚህ ጊዜ ዔሊ የዘጠና ስምንት ዓመት ሽማግሌ ነበር፤ ዓይኖቹ አጥርተው አያዩም ነበር፥ ማየትም አይችልም ነበር። 16 ሰውየውም ዔሊን፥ “ከውጊያው መስመር የመጣሁት እኔ ነኝ። ዛሬ ከውጊያው ሸሽቼ መጣሁ” አለው። ዔሊም፥ “ልጄ ሆይ፥ ነገሩ እንዴት እየሆነ ነው?” አለው። 17 ወሬውን ያመጣው ያ ሰው መልሶ፥ “እስራኤላውያን ከፍልስጥኤማውያን ፊት ሸሹ። ደግሞም በሕዝቡ መካከል ታላቅ ዕልቂት ሆኗል። ሁለቱ ወንዶች ልጆችህ፥ አፍኒን እና ፊንሐስ ሞተዋል፥ የእግዚአብሔር ታቦትም ተወስዷል” አለው። 18 እርሱም የእግዚአብሔርን ታቦት ጠቅሶ በተናገረ ጊዜ፥ ዔሊ በመግቢያው በር አጠገብ ከተቀመጠበት ወንበር ላይ ወደ ኋላው ወደቀ። ስላረጀና ውፍረት ስለነበረው አንገቱ ተሰብሮ ሞተ። እርሱም በእስራኤላውያን ላይ ለአርባ ዓመታት ፈርዶ ነበር። 19 በዚህ ጊዜ ምራቱ የፊንሐስ ሚስት አርግዛ የመውለጃ ሰዓቷ ደርሶ ነበር። የእግዚአብሔር ታቦት መማረኩን፥ ዐማቷና ባሏ መሞታቸውን በሰማች ጊዜ ተንበርክካ ወለደች፥ ነገር ግን ምጡ አስጨነቃት። 20 ለመሞት በምታጣጥርበት ጊዜ ያዋልዷት የነበሩ ሴቶች፥ "ወንድ ልጅ ወልደሻልና አትፍሪ“ አሏት። እርሷ ግን አልመለሰችላቸውም ወይም የነገሯትን በልቧ አላኖረችውም። 21 እርሷም የእግዚአብሔር ታቦት ስለተማረከና ስለ ዐማቷና ስለ ባልዋ "ክብር ከእስራኤል ተለየ!" ስትል ልጁን ኤካቦድ ብላ ጠራችው። 22 እርሷም፥”የእግዚአብሔር ታቦት ስለተማረከ ክብር ከእስራኤል ተለየ!" አለች።



1 Samuel 4:1

አቤንኤዘር … አፌቅ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

እስራኤላውያን በፍልጥኤማውያን ተሸነፉ የተገደሉትም

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "ፍልስጥኤማውያን እስራኤላውያንን አሸነፉ ገደሏቸውም' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

አራት ሺህ የሚያህሉ ሰዎችን

በዚህ ስፍራ አራት ሺህ የሚለው ቁጥር የሚጠጋጋ ቁጥር ነው፡፡ ከዚያ ቁጥር በጥቂት ከፍም ዝቅም ሊል ይችላል፡፡ የሚያህሉ የሚለው ቁርጥ ያለ ቁጥር እንዳልሆነ አመላካች ነው፡፡ አት፡- "አራት ሺህ የሚያህሉ ሰዎች' (ቀጥሮች ተመልከት)

1 Samuel 4:3

ሕዝቡ

ጦርነቱን ይዋጉ የነበሩ ወታደሮች

እግዚአብሔር በፍልስጥኤማውያን ፊት ስለ ምን መታን? ከጠላቶቻችንም … እናምጣ

ሽማግሌዎቹ በእርግጥ እግዚአብሔር ለምን እንደመታቸው አላወቁም ነበር፣ ነገር ግን ከእነርሱ ጋር እንዲሆን የቃል ኪዳኑን ታቦታ በማምጣት እንዴት በእርግጠኛነት ሁለተኛ እንዳይደገም እደሚያደርጉ እንደሚያውቁ በስህተት አሰቡ፡፡

በኪሩቤልም ላይ የሚቀመጠውን

ኪሩቤል በቃል ኪዳኑ ታቦት መክደኛ ላይ የሚገኙ እንደሆኑ ግልጽ ማድረግ ያስፈልግሃል፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች እግዚአብሔር በላይ በሰማይ በዙፋኑ እንደተቀመጠ ሁሉ የቃልኪዳኑ ታቦት አግዚአብሔር እግሩን የሚያኖርበት የእግሩ መረገጫ እንደሆነ በአብዘኛው ይናገራሉ፡፡ አት፡- "በቃል ኪዳኑ ታቦት ከኪሩቤል በላይ በዙፋኑ ላይ የተቀመጠው' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ይልተደረገ መረጃ ተመልከት)

የት ነበሩ

በሴሎ ነበሩ

1 Samuel 4:5

የእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ታቦት ወደ ሰፈር በገባ ጊዜ

"ሕዝቡ የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት ወደ ሰፈር ባመጡ ጊዜ' ትርጉሙን ግልጽ ለማድረግ ለመረዳት ምቹ የሆነ መረጃን ለመጨመር ጥቂት መግለጫዎች አስፈላጊ ናቸው፡፡ አት፡- "ሕዘቡ ከአፍኒንና ከፊንሐስ ጋር የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት ተሸከሙ ወደ ሰፈርም አመጡት፡፡' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

የእግዚአብሔር ታቦት ወደ ሰፈር ገባ

"ሕዝቡ የእግዚአብሔርን ታቦት ወደ ሰፈር አመጡት'

1 Samuel 4:7

አሉ … አሉ

"ለራሳቸው አሉ … ለእርስ በእርሳቸው አሉ' ወይም "ለእርስ በእርሳቸው አሉ … ለእርስ በእርሳቸው አሉ'ሁለተኛው ሐረግ ፍልስጥኤማውያን ለርስ በርሳቸው ያሉትን በግልጽ ያመለክታል፡፡ የመጀመሪያው ሐረግ ግን ወይ ያሰበቱን ወይም ለእርስ በእርሳቸው ያሉትን ሊያመለክት ይችላል፡፡ ከተቻለ ለማን እንደተነገረ አታመልክት፡፡

እግዚአብሔር መጥቶአል

ፍልስጥኤማውያን በብዙ አማልክት ያመልካሉ፣ ስለዚህ ከእነዚያ አማልክት መካከል አንዱ ወይም የማያመልኩት አንዱ ወደ ሰፈር እንደመጣ አምነዋል፡፡ ሌላኛው ሊሆን የሚችለው ትርጉም "ያህዌ መጥቶአል' ሲሉ የእስራኤልን አምላክ መደበኛ ስም እየጠሩ ነበር የሚለው ነው፡፡ ምክንያቱም 4፡8 ስለ "አማልክት' ይናገራል፣ አንዳንድ ትርጉሞች "እግዚአብሔሮች መጥተዋል' ይላሉ፣ ይኄውም፣ "አማልክት መጥተዋል' ማለት ነው፡፡ (ተውላጠ ስሞች ተመልከት)

ከእነዚህ ኃያላን አማልክት እጅ ማን ያድነናል?

ይህ አሳብ ገላጭ ጥያቄ ጥልቅ ፍርሃት መግለጫ ነው፡፡ በገላጭ አባባል ሊጻፍ ይችላል፡፡ አት፡- "ከእነዚአህ ኃያላን አማልክት እጅ ሊያድነን የሚችል ማንም የለም፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄዎች ተመልከት)

እነዚህ አማልክት …የመቱ አማልክት

ምክንያቱም በቁጥር 7 አምላክ (ወይም እግዚአብሔር) የሚለው ቃል በነጠላ ቁጥር ነው፣ ሊሆኑ ከሚችሉ ብዙ አማልክት መካከል አንዳቸውን ወይም የእስራኤልን አምላክ መደበኛ ስም በመጠቀም "ይህ ኃያል እግዚአብሔር … የመታ እግዚአብሔር' በሚያመለክት መልኩ በርካታ ትርጉሞች "ይህ ኃያል አምላክ … የመታ አምላክ' ይላሉ፡፡ (ተውላጠ ስሞች ተመልከት)

ሰዎች ሁኑ

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "ብርቱዎች ሁኑ ተዋጉ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 4:10

እስራኤላም ተሸነፉ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ "እስራኤል' የሚለው የእስራኤልን ሠራዊት ያመለክታል፡፡ አት፡- "የእስራኤልን ሠራዊት አሸነፉ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ እና ተለዋጭ ስም ተመልከት)

የእግዚአብሔር ታቦት ተወሰደ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "ፍልስጥኤማውያን የእግዚአብሔርንም ታቦት ወሰዱ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

1 Samuel 4:12

ልብሱን ቀድዶ በራሱም ላይ ትቢያ ነስንሶ

ይህ በእስራኤል ባሕል ጥልቅ ሐዘን መግለጫ መንገድ ነው፡፡

ልቡ ተናውጦ ነበር

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር ሲሆን በጣም ፈርቶ ወይም ስለ አንድ ነገር ታውኮ ነበር ማለት ነው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ከተማይቱ ሁሉ

ይህ በከተማይቱ ያሉ ሰዎች ሁሉ ለሚለው ምትክ ቃል ነው፡፡ (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 4:14

ሰውዬው

"የብንያም ሰው'

1 Samuel 4:16

ልጄ

ዔሊ የሌላኛው ሰው እውነተኛ አባት አልነበረም፡፡ ዔሊ የሰውዬው አባት እንደሆነ አድርጎ መናገሩ እንዳልተበሳጨ ነገር ግን ሊመልስለት እንደሚገባ ለሰውዬው ለማሳየት ነው፡፡ (ዘይቤአዊ አነጋገር ተመልከት)

እስራኤል ከፍልስጥኤማውያን ፊት ሸሹ

ይህ ስለሆነው ነገር አጠቃላይ መግለጫ ነው፡፡ የቀሩት የሰውዬው ንግግሮች ዝርዝሩን ያቀርባሉ፡፡

ደግሞ በሕዝቡ ዘንድ … ሁለቱም ልጆችህ …

"አሁን አንድ የባሰ ነገር እነግርሃለሁ … አሁን አንድ የባሰ ነገር እነግርሃለሁ' ወይም "ሕዝቡ ብቻ አይደለም፣ ነገር ግን ሁለቱ ልጆችህም'

የእግዚአብሔር ታቦት ተወሰደ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "ፍልስጥኤማውያን የእግዚአብሔርን ታቦት ወሰዱ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

1 Samuel 4:18

ሰውዬው በጠቀሰ ጊዜ

ብንያማዊው ሰው በጠቀሰ ጊዜ

በጠቀሰ

"በተናገረ'

አንገቱ ተሰብረ

ይህ በአድራጊ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "ስለወደቀ አንገቱ ተሰበረ' ወይም "ሲወድቅ አንገቱን ሰበረ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

1 Samuel 4:19

ምራቱ

የዔሊ ምራት

የእግዚአብሔር ታቦት ተማረከ

ይህ በአድራጊ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- ፍልስጥኤማውያን የእግዚአብሔርን ታቦት ማረኩ (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

ያሉአትን በልባዋ አላኖረችውም

"ላሉት ምንም ትኩረት አልሰጠችም' ወይም "የተሻለ እንዲሰማት ፈቀደች'

1 Samuel 4:21

ኤካቦድ

ስሙ ሐረግ ሲሆን ክብር የለም ማለት ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ የአንድ ሰው ስም ስለ ግለሰቡ፣ ስለ ቦታ ወይም ስለ ሚያመለክተው ነገር መረጃ ይሰጣል፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ፡- ተመልከት)

የእግዚአብሔር ታቦት ስለ ተማረከ … የእግዚአብሔር ታቦት ተማርኳልና

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "ፍልስጥኤማውያን የእግዚአብሔርን ታቦት ስለማረኩ … ፍልስጥኤማውያን የእግዚአብሔርን ታቦት ከመማረካቸው የተነሣ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)


Chapter 5

1 ፍልስጥኤማውያንም የእግዚአብሔርን ታቦት በመማረክ ከአቤንኤዘር ወደ አሽዶድ አመጡት። 2 እነርሱም የእግዚአብሔርን ታቦት ማርከው ወደ ዳጎን ቤት ወስደው በዳጎን አጠገብ አቆሙት። 3 የአሽዶድ ሰዎች በቀጣዩ ቀን ማልደው በተነሡ ጊዜ፥ ዳጎን በእግዚአብሔር ታቦት ፊት በምድር ላይ በግምባሩ ተደፍቶ አዩ። ስለዚህ ዳጎንን አንሥተው በስፍራው መልሰው አቆሙት። 4 ነገር ግን በማግስቱ ማልደው በተነሡ ጊዜ፥ ዳጎን በእግዚአብሔር ታቦት ፊት በምድር ላይ በግምባሩ ተደፍቶ አዩ። በደጁ መግቢያ ውስጥ የዳጎን ራሱና እጆቹ ተሰብረው ወድቀው ነበር። የቀረው የዳጎን ሌላው የአካል ክፍሉ ብቻ ነበር። 5 ለዚህ ነው እስካሁን እንኳን የዳጎን ካህናትና ሌላ ማንኛውም ሰው በአሽዶድ ወደሚገኘው ወደ ዳጎን ቤት በሚመጣበት ጊዜ የዳጎንን ደጅ መግቢያ ሳይረግጥ የሚያልፈው። 6 የእግዚአብሔር እጅ በአሽዶድ ሰዎች ላይ ከብዶ ነበር። በአሽዶድና በዙሪያው ባሉት ላይ ጥፋትን በማምጣት በእባጭ መታቸው። 7 የአሽዶድ ሰዎች የሆነባቸውን ባስተዋሉ ጊዜ፥ “እጁ በእኛና በአምላካችን በዳጎን ላይ ከብዳለችና የእስራኤል አምላክ ታቦት ከእኛ ጋር መቆየት የለበትም” አሉ። 8 ስለዚህ ወደ ፍልስጥኤማውያን ገዢዎች ልከው በአንድ ላይ ሰበሰቧቸው፤ እነርሱም፥ "በእስራኤል አምላክ ታቦት ላይ ምን እናድርግ?" አሏቸው። እነርሱም፥ “የእስራኤል አምላክ ታቦት ወደ ጌት ይምጣ” ብለው መለሱላቸው። የእስራኤልን አምላክ ታቦት ወደዚያ ወሰዱት። 9 ነገር ግን ወደዚያ ካመጡት በኋላ የእግዚአብሔር እጅ በከተማዪቱ ላይ ሆነ፥ ታላቅ መደናገርንም አደረገባቸው። ልጅና ዐዋቂውን፥ የከተማውን ሰዎች አስጨነቀ፤ ሰውነታቸውም በእባጭ ተወረረ። 10 ስለዚህ የእግዚአብሔርን ታቦት ወደ አቃሮን ላኩት። ነገር ግን የእግዚአብሔር ታቦት ወደ አቃሮን እንደ መጣ፥ አቃሮናውያን፥ "እኛንና ሕዝባችንን እንዲገድል የእስራኤልን አምላክ ታቦት ወደ እኛ አምጥተዋል" በማለት ጮኹ። 11 ስለዚህ ወደ ፍልስጥኤማውያን ገዢዎች በመላክ ሁሉንም በአንድ ላይ ሰበሰቧቸው፤ እነርሱም፥ “እኛንና ሕዝባችንን እንዳይገድል የእስራኤልን አምላክ ታቦት ላኩት፥ ወደ ስፍራውም ይመለስ" አሏቸው። በዚያ የእግዚአብሔር እጅ እጅግ ስለበረታባቸው በከተማው ሁሉ የሞት ድንጋጤ ነበረ። 12 ከሞት የተረፉት ሰዎች በእባጮቹ ይሠቃዩ ስለነበር የከተማዪቱ ጩኸት ወደ ሰማያት ወጣ።



1 Samuel 5:1

አሁን

ቃሉ የታሪኩ አዲስ ክፍል መጀመሩን ያሳያል፡፡ ቋንቋህ ተመሳሳይ ትርጉም የሚሰጥ ቃል ወይም ሐረግ ካለ በዚህ ስፍራ ልትጠቀም ትችላለህ፡፡

የእግዚአብሔር ታቦት

ይህንን በ1ሳሙኤል 3፡3 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ ይህ በ1ሳሙኤል 4፡3-4 "የእግዚአብሔር የኪዳኑ ታቦት' ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡

የዳጎን ቤት

ይህ የፍልስጥኤማውያንን አምላክ የዳጎንን ቤተ ጣዖት የሚያመለክት ነው፡፡

እነሆም ዳጎን

"ዳጎንን ለማየት እጅግ በአድናቆት ነበሩ'

ዳጎን በምድር ላይ በግምባሩ ወድቆ ነበር

እግዚአብሔር በሌሊት ሐውልቱ በግምባሩ እንዲወድቅ እንዳደረገ አንባቢው ማስተዋል አለበት፡፡ (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 5:4

ዳጎን ወደቀ

እግዚአብሔር ዳጎንን እንዲወድቅ እንዳደረገ አንባባዊ ማስተዋል አለበት፡፡

የዳጎን ራስ እጆቹም ተቆርጠው ወድቀው ነበር

እግዚአብሔር ጠላቱን እንዳሸነፈና የጠላቱን ራስና እጆች እንደቆረጠ ወታደር ዓይነት ነበር፡፡

ስለዚህ፣ እስከ ዛሬ ድረስ

ጸሐፊው ከዋናው ታሪክ ወጣ ያለ ጥቂት የመነሻ ታሪክ መረጃ እየሰጠ ነው፡፡ (ታሪካዊ ዳራ መረጃ ተመልከት)

እስከ ዛሬ ድረስ

በዚህ ስፍራ "ዛሬ' የሚለው ቃል የሚያመለከትው ጸሐፊው መጽሐፉን እስከሚጽፈበት ድረስ የነበረውን ጊዜ ነው፡፡

1 Samuel 5:6

የእግዚአብሔርም እጅ በላያቸው ከበደች

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ "እግዚአብሔር በጽኑ ፈረደባቸው' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

እጢ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) ከቆዳ ስር የሚወጣ የሚያሰቃይ እባጭ ወይም 2) የአህያ ኪንታሮት

አዛጦንና ድንበሯን

የከተማይቱ ስም በከተማይቱ ለሚኖሩ ሰዎች ምትክ ስም ነው፡፡ "በአዛጦን የሚኖሩ ሰዎችና በአዛጦን ዙሪያ የሚኖሩ ሰዎች' (ምትክ ቃል ተመልከት)

የአዛጦን ሰዎች አወቁ

"የአዛጦን ሰዎች አስተዋሉ'

የእስራኤል አምላክ ታቦት

ይህንን በ1ሳሙኤል 3፡3 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ ይህ በ1ሳሙኤል 4፡3-4 "የእግዚአብሔር የኪዳኑ ታቦት' ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡

1 Samuel 5:8

የእግዚአብሔር እጅ በእነርሱ ላይ ሆነች

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር ቀጣቸው' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

በታናሹም በታላቁም

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) እድሜን የሚያሳይ ስዕላዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "በሁሉ እድሜ የሚገኙ ሰዎች' ወይም 2) ማኅበራዊ መደብን የሚያሳይ ስዕላዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "ከድሆችና ደካሞች አንስቶ እሰከ ባለጸጎቹና ብርቱዎቹ ሰዎች' (ስዕላዊ ንግግር ተመልከት)

እጢ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) ከቆዳ ስር የሚወጣ የሚያሰቃይ እባጭ ወይም 2) የአህያ ኪንታሮት 1ሳሙኤል 5፡6ን እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት፡፡

1 Samuel 5:10

ጮኹ

ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 5:11

የእስራኤል አምላክ ታቦት

ይህንን በ1ሳሙኤል 3፡3 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ ይህ በ1ሳሙኤል 4፡3-4 "የእግዚአብሔር የኪዳኑ ታቦት' ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡

የእስራኤል አምላክ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) የእስራኤልን አምላክ መደበኛ ስም እየጠሩ ነበር ወይም 2) "የእስራኤል አምላክ'፣ እስራኤል ከብዙ አማልክት መካከል አንዱን ያመልኩ እንደነበር ያምኑ ነበር፡፡ 1ሳሙኤል 5፡7 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

በከተማይቱ ሁሉ የሞት ድንጋጤ ነበር

"ሊሞቱ ስለሆነ የከተማይቱ ሰዎች ሁሉ ፈርተው ነበር'

የእግዘአብሔር እጅ በዚያ እጅግ ከብዳ ነበረች

እጁ የእግዚብሔር ሰዎችን ስለ መቅጣተ ምትክ ቃል ነው፡፡ "እግዚአብሔር በዚያ ሰዎችን እጅግ እየቀጣ ነበር' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ያልሞቱትም ሰዎች

ይህ በተጨባጭ ብዙ ሰዎች እንደሞቱ ያመላክታል፡፡ (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

እጢ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) ከቆዳ ስር የሚወጣ የሚያሰቃይ እባጭ ወይም 2) የአህያ ኪንታሮት 1ሳሙኤል 5፡6ን እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት፡፡

የከተማይቱ ጩኽት ወደ ሰማያት ወጣ

ከተማ የሚለው ቃል ለከተማው ሕዝብ ምትክ ቃል ነው፡፡ ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) "ወደ ሰማያት ወጣ' የሚለው ቃል "ታላቅ ነበር' ለሚለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "የከተማይቱ ሰዎች ድምፃቸውን በጣም ከፍ አድርገው ጮኹ' ወይም 2) "ሰማያት' የሚለው ቃል ለሕዝቡ አማልክት ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "የከተማይቱ ሕዝብ ወደ አማልክቶቻቸው ጮኹ' (ምትክ ቃልና ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)


Chapter 6

1 የእግዚአብሔር ታቦት በፍልስጥኤማውያን አገር ከተቀመጠ ሰባት ወር ሆነው። 2 ከዚያም የፍልስጥኤም ሰዎች ካህናትንና ጠንቋዮችን ጠርተው፥ “የእግዚአብሔርን ታቦት ምን እናድርገው? ወደ አገሩ እንዴት አድርገን መመለስ እንዳለብን ንገሩን” አሉአቸው። 3 ካህናቱና ጠንቋዮቹም፥ "የእስራኤልን አምላክ ታቦት መልሳችሁ የምትልኩ ከሆነ ያለስጦታ አትላኩት፤ በተቻለ መጠን የበደል መስዋዕትም ላኩለት። ከዚያም ትፈወሳላችሁ፥ እናንተም እስካሁን ድረስ እጁን ከላያችሁ ላይ ያላነሣው ለምን እንደሆነ ታውቃላችሁ"። 4 ሕዝቡም፥ “የምንመልሰው የበደል መስዋዕት ምን መሆን አለበት?”አሏቸው። እነርሱም እንዲህ በማለት መለሱላቸው፥ "አምስት የወርቅ እባጮችንና አምስት የወርቅ አይጦችን፥ በቁጥር አምስት መሆኑም የፍልስጥኤማውያንን ገዢዎች ቁጥር የሚወክል ነው። እናንተንና ገዢዎቻችሁን የመታው ተመሳሳይ መቅሰፍት ነውና። 5 ስለዚህ ምድራችንን ባጠፋው በእባጮቻችሁና በአይጦቻችሁ አምሳል ማድረግ አለባችሁ፥ ለእስራኤል አምላክም ክብርን ስጡ። ምናልባት እጁን ከእናንተ፥ ከአማልክቶቻችሁና ከምድሪቱ ላይ ያነሣ ይሆናል። 6 ግብፃውያንና ፈርዖን ልባቸውን እንዳደነደኑ ለምን ልባችሁን ታደነድናላችሁ? ያን ጊዜ ነበር የእስራኤል አምላክ ክፉን ያደረገባቸው፤ ታዲያ ግብፃውያኑ ሕዝቡን አልለቀቋቸውም?እነርሱስ ከዚያ አልወጡም? 7 እንግዲህ አዲስ ሠረገላና እስካሁን ቀንበር ያልተጫነባቸውን ሁለት የሚያጠቡ ላሞች አዘጋጁ። ላሞቹን በሠረገላው ጥመዷቸው፥ እምቦሳዎቻቸውን ግን ከእነርሱ ለይታችሁ በቤት አስቀሩአቸው። 8 ከዚያም የእግዚአብሔርን ታቦት ወስዳችሁ በሠረገላው ላይ አኑሩት። የበደል መስዋዕት አድርጋችሁ የምትመልሱለትን የወርቁን አምሳያዎች በሳጥን ውስጥ አድርጋችሁ በአንደኛው ጎኑ አስቀምጡ። ከዚያም ልቀቁትና በራሱ መንገድ እንዲሄድ ተዉት። 9 ከዚያም ተመልከቱ፥ ወደ ራሱ ምድር፥ ወደ ቤት ሳሚስ በመንገዱ ከሄደ፥ ይህንን ታላቅ ጥፋት ያመጣው እግዚአብሔር ነው ማለት ነው። ካልሆነ ግን፥ ይህ በአጋጣሚ የደረሰብን እንጂ የመታን የእርሱ እጅ እንዳልሆነ እናውቃለን"። 10 ሰዎቹም እንደተነገራቸው አደረጉ፤ ሁለት የሚያጠቡ ላሞችን ወሰዱና በሠረገላው ጠመዷቸው፥ እምቦሳዎቻቸውንም ከቤት እንዳይወጡ አደረጉ። 11 የወርቁን አይጥና የእባጮቻቸው ምሳሌ የሆነውን ከያዘው ሳጥን ጋር የእግዚአብሔርን ታቦት በሠረገላው ላይ አደረጉት። 12 ላሞቹም በቤት ሳሚስ አቅጣጫ ቀጥ ብለው ሄዱ። እነርሱም በዚያው ጎዳና፥ ወደ ግራም ወደ ቀኝም ሳይሉ ቁልቁል ሄዱ። የፍልስጥኤማውያን ገዢዎችም እስከ ቤት ሳሚስ ዳርቻ ድረስ ከበስተኋላቸው ተከተሏቸው። 13 በዚህ ጊዜ የቤት ሳሚስ ሰዎች በሸለቆው ውስጥ ስንዴአቸውን በማጨድ ላይ ነበሩ። ቀና ብለው ባዩ ጊዜ ታቦቱን ተመለከቱ፥ ደስም አላቸው። 14 ሠረገላው የቤት ሳሚስ ሰው ወደሆነው ወደ ኢያሱ እርሻ መጥቶ በዚያ ቆመ። በዚያም ትልቅ ቋጥኝ ነበር፥ የሠረገላውን እንጨት በመፍለጥ ላሞቹን ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት አድርገው አቀረቡ። 15 ሌዋውያኑ የእግዚአብሔርን ታቦትና አብሮት የነበረውን፥ የወርቁ ምስሎች የነበሩበትን ሳጥን፥ ከሠረገላው አውርደው በትልቁ ቋጥኝ ላይ አስቀመጡት። በዚያው ቀን የቤት ሳሚስ ሰዎች ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት አቀርቡ፥ መሥዋዕቶችንም ሠዉ። 16 አምስቱ የፍልስጥኤማውያን ገዢዎች ይህንን ባዩ ጊዜ በዚያው ቀን ወደ አቃሮን ተመለሱ። 17 የፍልስጥኤም ሰዎች ለእግዚአብሔር የበደል መስዋዕት አድርገው የመለሷቸው የወርቅ እባጮች እነዚህ ናቸው፤ አንዱ ስለ አሽዶድ፥ አንዱ ስለ ጋዛ፥ አንዱ ስለ አስቀሎና፥ አንዱ ስለ ጌት እና አንዱ ስለ አቃሮን ነበር። 18 የወርቁ አይጥ አምስቱ ገዢዎች ከሚገዟቸው የተመሸጉ የፍልስጥኤማውያን ከተሞችና መንደሮች ቁጥር ሁሉ ጋር ቁጥሩ ተመሳሳይ ነበር። የእግዚአብሔርን ታቦት ያስቀመጡበት ያ ታላቅ ቋጥኝ በቤት ሳሚስ በኢያሱ እርሻ ውስጥ እስከ ዛሬ ድረስ ምስክር ሆኖ ይኖራል። 19 ወደ ታቦቱ ውስጥ ተመልክተዋልና እግዚአብሔር ከቤት ሳሚስ ሰዎች ጥቂቶቹን መታቸው። እርሱም ሰባ ሰዎችን ገደለ። እግዚአብሔር ሕዝቡን ክፉኛ ስለመታቸው ሕዝቡ አለቀሱ። 20 የቤት ሳሚስ ሰዎችም፥ “በዚህ ቅዱስ አምላክ በእግዚአብሔር ፊት መቆም የሚችል ማነው? ከእኛስ ወደ ማን ይሄዳል?” አሉ። 21 በቂርያትይዓሪም ወደሚኖሩት መልዕክተኞች ልከው፥ “ፍልስጥኤማውያን የእግዚአብሔርን ታቦት መልሰዋል፤ ወደዚህ ውረዱና ውሰዱት” አሏቸው።



1 Samuel 6:1

ካህናትና ጠንቋይችን

እነዚህ ዳጎንን የሚያመልኩ የአሕዛብ ካህናትና ጠንቋዮች ናቸው፡፡

እንዴት እንደምንሰደው ንገሩን

ፍልስጥኤማውያን ከዚህ ወዲያ እግዚአብሔርን ሳያሰቆጡ ታቦቱን እንዴት እንደሚያስወግዱት ማወቅ ፈለጉ፡፡

1 Samuel 6:3

የእስራኤል አምላክ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) የእስራኤልን አምላክ መደበኛ ስም እየጠሩ ነበር ወይም 2) "የእስራኤል አምላክ'፣ እስራኤል ከብዙ አማልክት መካከል አንዱን ያመልኩ እንደነበር ያምኑ ነበር፡፡ 1ሳሙኤል 5፡7 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

የበደል መሥዋዕት መልሱለት እንጂ ባዶውን አትስደዱት

ባዶውን አትስደዱት የሚሉት ቃላት አንድን ነገር አጠንክሮ መናገሪያ መንገድ ናቸው፡፡ አት፡- "የበደል መሥዋዕት መስደድ አለባችሁ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ትፈወሳላችሁ

"ከእንግዲህ ወዲህ አትታመሙ'

እናንተ

እናንተ የሚለው ተውላጠ ስም የብዙ ቁጥር እንደመሆኑ ፍልስጥኤማውያንን ሁሉ ያመለክታል፡፡ (አንተ/እናንተ ተመልከት)

እጁ ከእናንተ አለመራቁ ስለምን ነው

በዚህ ስፍራ "እጅ' የሚለው ቃል እግዚአብሔር መከራን ለማምጣትና ለመቅጣት ያለውን ኃይል ለመግለጽ ጥቅም ላይ የዋለ ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "መከራችሁን ለምን አላቀለላችሁም' (ምትክ ቃል ተመልከት)

እጢ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) ከቆዳ ስር የሚወጣ የሚያሰቃይ እባጭ ወይም 2) የአህያ ኪንታሮት 1ሳሙኤል 5፡6ን እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት፡፡

አይጦች

ከአንድ በላይ አይጥ

1 Samuel 6:5

ምሳሌዎች

ምሳሌ እውነተኛው ነገር የሚመስል ነገር ነው፡፡

እጢ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) ከቆዳ ስር የሚወጣ የሚያሰቃይ እባጭ ወይም 2) የአህያ ኪንታሮት 1ሳሙኤል 5፡6ን እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት፡፡

የሚያወድሙ

"የሚያጠፉ'

የእስራኤል አምላክ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) የእስራኤልን አምላክ መደበኛ ስም እየጠሩ ነበር ወይም 2) "የእስራኤል አምላክ'፣ እስራኤል ከብዙ አማልክት መካከል አንዱን ያመልኩ እንደነበር ያምኑ ነበር፡፡ 1ሳሙኤል 5፡7 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

እጁን ከእናንተና ከአማልክቶቻችሁ፣ ከምድራችሁም ያነሳል

በዚህ ስፍራ "እጅ' የሚለው ቃል እግዚአብሔር መከራን ለማምጣትና ለመቅጣት ያለውን ኃይል ለመግለጽ ጥቅም ላይ የዋለ ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "እናንተን፣ አማልክቶቻችሁንና ምድራችሁን መቅጣት ያቆማል' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ግብጻውያንና ፈርዖንም ልባቸውን እንዳደነደኑ ልባችሁን ለምን ታደነድናላችሁ?

ካህናቱና ጠንቋዮቹ አሳብ ገላጭ ጥያቄ በመጠቀም፣ እግዚአብሔርን መታዘዝ እምቢ ካሉ ምን ሊሆን እንደሚችል ትኩረት ሰጥተው እንዲያስቡ ፍልስጥኤማውያንን አጥብቀው እያስገነዘቡ ነው፡፡ (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ልባችሁን ታደነድናላችሁ

ይህ ግትር መሆንና ለእግዚብሔር ፈቃድ አለመታዘዝ የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ግብጻውያን ሕዝቡን አልሰደዱአቸውምን እነርሱም አልሄዱምን?

ይህ እግዚአብሔር በግብጻውያን ላይ መከራ ማምጣቱን እንዲያቆም በስተመጨረሻ ግብጻውያን እንዴት እስራኤላውያን ከግብጽ እንዲወጡ እንዳደረጉ ፍልስጥኤማውያንን ለማሳሳብ የተጠቀሙበት አሳብ ገላጭ ጥያቄ ነው፡፡ (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

1 Samuel 6:7

ሁለት የሚያጠቡ ላሞች

እስከ አሁን ወተት የሚጠጡ ጥጆች ያሉአቸው ሁለት ላሞች

ይሄድም ዘንድ ስደዱት

እንደተለመደው ሁለቱ ላሞች ወደ ጥጆቻቸው ወደ ቤት መመለስ ይኖርባቸው ነበር፡፡

ወደ ቤትሳሚስ ከሄደ … እግዚአብሔር ነው

ላሞቹ ጥጆቻቸው በስተኋላ በፍልስጥኤማውያን ሰፈር እያሉ ወደ ቤትሳሚስ ለመንከራተት ይመርጣሉ ብሎ ማሰብ የማይመስል ነው፡፡

1 Samuel 6:10

ሁለት የሚያጠቡ ላሞች

እስከ አሁን ወተት የሚጠጡ ጥጆች ያሉአቸው ሁለት ላሞች፡፡ 1ሳሙኤል 6፡7ን እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

አይጦች

ይህን በ1ሳሙኤል 6፡4 እንዳለው ተርጉም፡፡

የእባጮቻቸውን ቅርጾች

"የእባጮቻቸውን ምሳሌዎች'

እጢ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) ከቆዳ ስር የሚወጣ የሚያሰቃይ እባጭ ወይም 2) የአህያ ኪንታሮት 1ሳሙኤል 5፡6ን እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት፡፡

ላሞቹ ወደ ቤትሳሚስ አቅጣጫ አቅንተው ሄዱ

በአብዛኛው የሚያጠቡ ላሞች ወደ ጥጆቻቸው ይመለሳሉ፣ ነገር ግን እነዚህ ላሞች ወደ ቤትሳሚስ ሄዱ፡፡

እምቧ እያሉ ሄዱ

እምቧ ማለት ላሞች በድምጻቸው የሚፈጥሩት ጩኸት ነው፡፡

ወደ ቀኝም ወደ ግራም አላሉም

"ከአውራ ጎዳናው አልወጡም፡፡' ይህ በአዎንታ እንደሚከተለው ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "በአውራው ጎዳና ዘለቁ' ወይም "ቀጥ ብለው ወደ ፊት ይሄዱ ነበር'

1 Samuel 6:13

አሁን

ቃሉ የታሪኩ አዲስ ክፍል መጀመሩን ያሳያል፡፡ ቋንቋህ ተመሳሳይ ትርጉም የሚሰጥ ቃል ወይም ሐረግ ካለ በዚህ ስፍራ ልትጠቀም ትችላለህ፡፡

የቤትሳሚስ ሰዎች

እስራኤላውያን ነበሩ፡፡

ዓይናቸውን ከፍ አድርገው

ይህ ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "አሻቅበው አዩ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 6:14

ታላቅ ድንጋይ በዚያ ነበር

ሰዎች ላሞቻቸውን ሲሰው ይህን ድንጋይ እንደ መሠዊያ ይጠቀሙበት ነበር፡፡

ሌዋውያኑ የእግዚአብሔርን ታቦት አወረዱ

ይህ የሆነው ላሞቹን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርጎ ለማቅረብ ሰረገላውን ለማንደንድ ከመፍለጣቸው በፊት ነው፡፡

ከእርሱ ጋር የነበረውን የወርቅ ዕቃ ያለበትን

ሳጥኑ የአይጥና የእባጭ የወርቅ ምሳሌዎች ይዟል

1 Samuel 6:16

የፍልስጥኤማውያን አምስቱ አለቆች

"የፍልስጥኤማውያን አምስቱ ነገሥታት'

1 Samuel 6:17

እጢ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጎሞች፡- 1) ከቆዳ ስር የሚወጣ የሚያሰቃይ እባጭ ወይም 2) የአህያ ኪንታሮት 1ሳሙኤል 5፡6ን እንዴት እንደተረጎምክ ተመልከት፡፡

አይጦች

ይህን በ1ሳሙኤል 6፡4 እንዳለው ተርጉም፡፡

የተመሸጉ ከተሞች

በውስጥ ያለውን ሕዝብ ከጠላቶቻቸው ጥቃት ለመጠበቅ በዙሪያቸው ትላልቅ ቅጥች የተገነቡላቸው ከተሞች ናቸው፡፡

ታላቁም ድንጋይ እስከ ዛሬ ድረስ ምስክር ሆኖ አለ

ድንጋዩ ማየት እንደሚችል እንደ አንድ ግለሰብ ተጠቅሷል፡፡ አት፡- "ታላቁ ድንጋይ … እስከ ዛሬ ድረስ በዚያ አለ፣ሰዎችም በላዩ ላይ የተፈጸመውን ያስታውሳሉ፡፡' (ግዑዝ ነገርን እንደ ሰው ማየትን ተመልከት)

ኢያሱ

የሰው ስም (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ቤትሳሚሳውያን

ይህ ከቤትሳሚስ የሆነ ሰው የሚጠራበት ነው፡፡ አት፡- "ከቤትሳሚስ' (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

እስከ ዛሬ ድረስ

ጸሐፊው መጽሐፉን እስከጻፈበት ጊዜ ድረስ

1 Samuel 6:19

ወደ ታቦቱ ውስጥ ተመልክተዋል

ታቦቱ እጅግ ቅዱስ ስለ ነበር ማንም ወደ ውስጥ እንዲመለከት አልተፈቀደለትም፡፡ ታቦቱን እንኳን ለማየት የተፈቀደላቸው ካህናት ብቻ ናቸው፡፡

50,070 ሰዎች

"አምሳ ሺህ እና ሰባ ሰዎች' (ቁጥሮች ተመልከት)

በዚህ ቅዱስ አምላክ በእግዚአብሔር ፊት መቆም ማን ይችላል?

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፣ 1) ሕዝቡ ስለ እግዚብሔር ያደረበትን ፍርሃት ለመግለጽ አሳብ ገላጭ ጥያቄ ነው፡፡ አት፡- "ቅዱስ ስለሆነ እግዚአብሔርን መቋቋም የሚችል ማንም የለም!' ወይም 2) መረጃ ለማግኘት የቀረበ ጥያቄ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት መቆም የሚለው ሐረግ እግዚአብሔርን የሚያገለግሉ ካህናትን የሚያመለክት ነው፡፡ ሕዝቡ እግዚአብሔር ታቦቱን እንዲይዝ የፈቀደለትን ካህን እፈለገ መሆኑን ያመላክታል፡፡ አት፡- "በመካከላችን ይህን ቅዱስ አምላክ፣ ያህዌን ማገልገልና ታቦቱን ማስተዳደር የሚችል ካህን አለን?' (አሳብ ገላጭ ጥያቄዎችንና እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ታቦቱ ከእኛ ወደ ማን ይሄዳል?

መረጃ ለማግኘት የቀረበ ጥያቄ ነው፡፡ ሁለተኛ እንዳይቀጣቸው እግዚአብሔርና ታቦቱ ወደ አንድ ቦታ እንዲሄዱ ሕዝቡ እንደፈለገ ይጠቁማል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር ሁለተኛ እንዳይቀጣን ይህን ታቦት ወዴት መስደድ እንችላለን?' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 6:21

ቂርያትይዓሪም

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)


Chapter 7

1 የቂርያትይዓሪም ሰዎች መጥተው የእግዚአብሔርን ታቦት ወሰዱ፥ በኮረብታው ላይ ወዳለው ወደ አሚናዳብ ቤት አስገቡት። የእግዚአብሔርን ታቦት እንዲጠብቅ ልጁን አልዓዛርን ለዚህ አገልግሎት ለዩት። 2 ታቦቱ በቂርያትይዓሪም ከተቀመጠ ብዙ ዓመት አለፈው፥ ሃያ ዓመትም ሆነው። የእስራኤል ቤት ሁሉ አዘኑ፥ ወደ እግዚአብሔር ለመመለስም ፈለጉ። 3 ሳሙኤል የእስራኤልን ሕዝብ በሙሉ እንዲህ አላቸው፥ "በሙሉ ልባችሁ ወደ እግዚአብሔር የምትመለሱ ከሆነ እንግዶቹን አማልክትና አስታሮትን ከመካከላችሁ አስወግዱ፥ ልባችሁን ወደ እግዚአብሔር መልሱ፥ እርሱንም ብቻ አምልኩት፥ ያን ጊዜ ከፍልስጥኤማውያን እጅ ያድናችኋል"። 4 ከዚያም የእስራኤል ሕዝብ በኣልንና አስታሮትን አስወገዱ፥ እግዚአብሔርን ብቻም አመለኩ። 5 ከዚያም ሳሙኤል፥ "እስራኤልን በሙሉ ምጽጳ ላይ ሰብስቡ፥ እኔም ስለ እናንተ ወደ እግዚአብሔር እጸልያለሁ“ አላቸው። 6 እነርሱም በምጽጳ ተሰበሰቡ፥ ውሃም ቀድተው በእግዚአብሔር ፊት አፈሰሱ። በዚያም ቀን ጾሙ፥”በእግዚአብሔር ላይም ኃጢአትን አድርገናል“ አሉ። ሳሙኤል በእስራኤል ሕዝብ ላይ የፈረደውና ሕዝቡን የመራው በዚያ ነበር። 7 የእስራኤል ሕዝብ በምጽጳ መሰብሰባቸውን ፍልስጥኤማውያን በሰሙ ጊዜ፥ የፍልስጥኤማውያን ገዢዎች እስራኤልን ለማጥቃት መጡ። የእስራኤል ሰዎች ይህንን በሰሙ ጊዜ ፍልስጥኤማውያንን ፈሩ። 8 ከዚያም የእስራኤል ሕዝብ ሳሙኤልን፥”ከፍልስጥኤማውያን እጅ እንዲያድነን፥ ስለ እኛ ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር መጣራትህን አታቁም“ አሉት። 9 ሳሙኤል የሚጠባ ግልገል ወስዶ ለእግዚአብሔር ሙሉውን የሚቃጠል መስዋዕት አድርጎ ሠዋው። ከዚያም ሳሙኤል ስለ እስራኤል ወደ እግዚአብሔር ጮኸ፥ እግዚአብሔርም መለሰለት። 10 ሳሙኤል የሚቃጠለውን መስዋዕት በማቅረብ ላይ እያለ ፍልስጥኤማውያን እስራኤልን ለማጥቃት ቀረቡ። ነገር ግን በዚያን ቀን እግዚአብሔር በፍልስጥኤማውያን ላይ በታላቅ ድምፅ አንጎደጎደባቸው፥ አሸበራቸውም፥ በእስራኤልም ፊት ተሸንፈው ሸሹ። 11 የእስራኤል ሰዎችም ከምጽጳ ተነሥተው ፍልስጥኤማውያንን አሳደዱ፥ ከቤትካር በታች እስካለው ቦታ ድረስ ተከትለው ገደሏቸው። 12 ከዚያም ሳሙኤል አንድ ድንጋይ አንሥቶ በምጽጳና በሼን መካከል አቆመው።”እስካሁን ድረስ እግዚአብሔር ረድቶናል“ በማለት አቤንኤዘር ብሎ ጠራው። 13 ስለዚህ ፍልስጥኤማውያን ተሸነፉ፥ የእስራኤልን ድንበርም አልፈው አልገቡም። በሳሙኤል የሕይወት ዘመን ሁሉ የእግዚአብሔር እጅ በፍልስጥኤማውያን ላይ ከብዳ ነበር። 14 ፍልስጥኤማውያን ከእስራኤል የወሰዷቸው ከአቃሮን እስከ ጌት ያሉ መንደሮች ለእስራኤል ተመለሱላቸው፤ እስራኤላውያን ድንበሮቻቸውን ከፍልስጥኤማውያን አስመለሱ። በዚያን ጊዜ በእስራኤላውያንና በአሞራውያን መካከል ሰላም ነበረ። 15 ሳሙኤል በሕይወት ዘመኑ ሁሉ በእስራኤል ላይ ፈረደ። 16 በየዓመቱ ወደ ቤቴል፥ ወደ ጌልገላና ወደ ምጽጳ ይዘዋወር ነበር። በእነዚህ ስፍራዎች ሁሉ በእስራኤላውያን መካከል ባሉ አለመግባባቶች ላይ ይፈርድ ነበር። 17 ከዚያም መኖሪያው በዚያ ነበርና ወደ ራማ ይመለስ ነበር፤ በዚያም ደግሞ በእስራኤላውያን አለመግባባት ላይ ይፈርድ ነበር። በዚያም ደግሞ ለእግዚአብሔር መሠዊያን ሠራ።



1 Samuel 7:1

ቂርያትይዓሪም

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

አሚናዳብ … አልዓዛር

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

ሀያ ዓመታት

20 ዓመታት (ቁጥሮች ተመልከት)

1 Samuel 7:3

የእስራኤል ቤት ሁሉ

"ቤት' የሚለው ቃል በቤት ውስጥ የሚኖሩትን ሰዎችና ትውልዳቸውን የሚያመለክት ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "የእስራኤል ትውልድ' ሁሉ ወይም "የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ' (ምትክ ቃል ተመልከት)

በሙሉ ልባችሁ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ

በዚህ ስፍራ "በሙሉ ልብ' የሚለው ለአንድ ነገር ፈጽሞ መሰጠት የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "እግዚአብሔርን ብቻ ለማምለክና ለመታዘዝ ፈጽማችሁ የተሰጣችሁ ሁኑ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመለክት)

1 Samuel 7:5

እስራኤል ሁሉ

"የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ' ወይም "እስራኤላውያን ሁሉ'

ውኃ ቀድተው በእግዚአብሔር ፊት አፈሰሱ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) ሕዝቡ የጾም ክፍል አድርገው የራሳቸውን ወኃ አልተጠቀሙም ወይም 2) ከምንጭ ወይም ከጉድጓድ ውኃ አገኙ፣ በኃጢታቸውም ለመጸጸታቸው እንደ ውጪያዊ ምልክት በምድር ላይ አፈሰሱት፡፡ (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 7:7

የፍልስጥኤማውያን አለቆች በእስራኤል ላይ ጥቃት አደረሱ

በእስራኤል ላይ ጥቃት ያደረሱት ሠራዊቶቹ እንጂ አለቆቹ ራሳቸው እንዳልሆኑ በግልጽ ማስቀመጥ ይቻላል፡፡ አት፡- "የፍልስጥኤማውየን አለቆች ሠራዊታቸውን እየመሩ በእስራኤል ላይ ጥቃት አደረሱ' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ከፍልስጥኤማውያን እጅ አድነን

እጅ የሰውዬውን ኃይል የሚያሳይ ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "ከፍልስጥኤማውያን ሠረዊት አድነን' ወይም "የፍልስጥኤማውያን ሠራዊት እንዳይጎዱን አድርግ' (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 7:9

የሚጠባ የበግ ጠቦት

እስካሁን ድረስ የእናቱን ወተት የሚጠጣ ጠቦት

ጮኸ

"ለእርዳታ ጮኸ'

እግዚአብሔር መለሰለት

"እንዲያደርግ ሳሙኤል የጠየቀውን እግዚአብሔር አደረገ'

1 Samuel 7:10

ሳሙኤልም … በቤትካር

ይህ ጸሐፊው "እግዚአብሔር መለሰለት' ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ ያብራራል (1ሳሙኤል 7፡9)

ግራ አጋባቻው

"ግራ መጋባት' የሚለው ቃል በዚህ ስፍራ ጥቅም ላየ የዋለው ፍልስጥኤማውያን በግልጽ ማሰብ አልቻሉም ለማለት ነው፡፡ አት፡- "በግልጽ ማሰብ እንዳይችሉ አደረጋቸው' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

በእስራኤልም ፊት ድል ተመቱ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) እግዚአብሔር በእስራኤል ፊት ድል መታቸው ወይም 2) እስራኤል ድል መታቸው (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

ድል መምታት

ሰዎችን ድል መምታት ማለት ምንም ጉዳት ከማድረሳቸው በፊት ማሸነፍ ነው፡፡

ቤትካር

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 7:12

ድንጋይ ወስዶ አኖረ

በዚያ ምድር እስራኤላውያንን ሌሎች ሕዝቦች አስፈላጊ ነገሮች ሲሆኑ ለእግዚአብሔር እርዳታ ማስታወሻ እንዲሆን ትልቅ ድንጋይ ያኖራሉ፡፡

ምጽጳ … ሼን

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 7:13

ፍልስጥኤማውያን ተገዙ

ጸሐፊው እንዴት ፍልስጥኤማውያን እንዴት በቁጥጥር ስር እንደዋሉ መናገሩን ፈጸመ፡፡ ቋንቋህ ትረካን የሚደመድምበት መንገድ ካለው እዚህ ጋ መጠቀም ትችላለህ፡፡

ፍልስጥኤማውያን ተገዙ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "እግዚብሔርን ፍልስጥኤማውያንን አስገዛቸው' ወይም "እግዚአብሔር ፍልስጥኤማውያንን ጉዳት ከማድረስ አገዳቸው' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

ወደ እስራኤል ድንበር አልመጡም

ፍልስጥኤማውያን ሊያጠቁአቸው ወደ እስራኤል ድንበር አይገቡም ነበር፡፡

የእግዚአብሔር እጅ በፍልስጥኤማውያን ላይ ነበረች

እጅ የሚለው ቃል ለኃይል ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር በፍልስጥኤማውያን ላይ ኃይሉን ይጠቀም ነበር' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ከተሞች … ከእስራኤል ለእስራኤል ተመለሱ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) በዚህ ስፍራ "እስራኤል' የሚለው ቃል የሚያመለከትው የእስራኤልን "ምድር' ነው፡፡ ከእስራኤል … እግዚአብሔር ከተሞችን ለእስራኤል ምድር መለሰ ወይም 2) "እስራኤል' የሚለው ቃል በዚያ ለሚኖረው ሕዝብ ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "ከእስራኤል … የእስራኤል ሕዝብ ከተሞቹን የኔ ናቸው ማለት ቻለ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽና ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 7:15

ይዞር ነበር

በአስቸጋሪ ዙር ከቦታ ቦታ ይጓዝ ነበር

በሙግቶች ላይ ይወስን ነበር

ሙግት ማለት ክርክር ወይም በሁለት ወይም ከዚያ በላይ በሆኑ ሰዎች መካከል የሚፈጠር አለመስማማት ነው፡፡


Chapter 8

1 ሳሙኤል በሸመገለ ጊዜ ልጆቹን በእስራኤል ላይ ፈራጆች አድርጎ ሾማቸው። 2 የመጀመሪያ ልጁ ስም ኢዮኤል፥ የሁለተኛው ስም አብያ ነበር። እነርሱም በቤርሳቤህ ፈራጆች ነበሩ። 3 ነገር ግን ልጆቹ ነውረኛ ጥቅም ፈላጊዎች ሆኑ እንጂ በእርሱ መንገድ አልሄዱም። ጉቦ እየተቀበሉ ፍትሕን አዛቡ። 4 ከዚያም የእስራኤል ሽማግሌዎች በአንድነት ተሰብስበው በራማ ወደሚኖረው ወደ ሳሙኤል መጡ። 5 እነርሱም፥ "ተመልከት፥ አንተ ሸምግለሃል፥ ልጆችህም በመንገድህ አይሄዱም። እንደ ሌሎች ሕዝቦች ሁሉ እንዲፈርድልን ንጉሥ አንግሥልን" አሉት። 6 ነገር ግን፥ “እንዲፈርድልን ንጉሥ ስጠን” ባሉት ጊዜ ነገሩ ሳሙኤልን ቅር አሰኘው። ስለዚህ ሳሙኤል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። 7 እግዚአብሔርም ሳሙኤልን እንዲህ አለው፥ “በላያቸው ላይ ንጉሥ እንዳልሆን የተቃወሙት እኔን እንጂ አንተን አይደለምና በሚሉህ ነገር ሁሉ የሕዝቡን ቃል ታዘዝ። 8 ከግብፅ ካወጣዃቸው ጊዜ ጀምሮ እኔን ትተው ሌሎች አማልክቶችን በማምለክ ሲያደርጉት የነበረውን ያንኑ አሁን እያደረጉ ነው፤ በአንተም ላይ የሚያደርጉት እንደዚሁ ነው። 9 አሁንም የሚሉህን ስማቸው፤ ነገር ግን በላያቸው የሚገዛው ንጉሥ የሚያደርግባቸውን እንዲያውቁ አጥብቀህ አስጠንቅቃቸው"። 10 ስለዚህ ሳሙኤል ንጉሥ ለጠየቀው ሕዝብ የእግዚአብሔርን ቃል በሙሉ ነገራቸው። 11 እርሱም እንዲህ አላቸው፥ "ንጉሡ በላያችሁ ላይ የሚገዛው እንዲህ ነው። ወንዶች ልጆቻችሁን ወስዶ ፈረሰኞች እንዲሆኑና በሠረገላዎቹ ፊት እንዲሮጡ በሠረገላዎቹ ላይ ይሾማቸዋል። 12 እርሱም ለራሱ ሻለቃዎችንና ሃምሳ አለቃዎችን ይሾማል። አንዳንዶቹ መሬቱን እንዲያርሱ፥ ሌሎቹም እህሉን እንዲያጭዱ፥ አንዳንዶቹ የጦር መሳሪያዎችንና ሌሎቹም የሠረገላ ዕቃዎችን እንዲሠሩለት ያደርጋቸዋል። 13 ሴቶች ልጆቻችሁን ደግሞ ሽቶ ቀማሚዎች፥ ወጥ ሠሪዎችና እንጀራ ጋጋሪዎች እንዲሆኑ ይወስዳቸዋል። 14 በጣም ምርጥ የሆነውን መሬታችሁን፥ የወይን ቦታችሁንና የወይራ ዛፋችሁን ወስዶ ለአገልጋዮቹ ይሰጣቸዋል። 15 ከእህላችሁና ከወይናችሁ አንድ ዐሥረኛውን ወስዶ ለሹማምንቱና ለአገልጋዮቹ ይሰጣቸዋል። 16 ወንዶችና ሴቶች አገልጋዮቻችሁን፥ ከወጣት ልጆቻችሁና ከአህዮቻችሁ የተመረጡትን ይወስዳል፤ ሁሉንም ለእርሱ እንዲሠሩ ያደርጋቸዋል። 17 ከበግና ከፍየል መንጋዎቻችሁ አንድ ዐሥረኛውን ይወስዳል፥ እናንተም አገልጋዮቹ ትሆናላችሁ። 18 በዚያም ቀን ለራሳችሁ ስለመረጣችሁት ንጉሥ ታለቅሳላችሁ፤ ነገር ግን በዚያን ቀን እግዚአብሔር አይመልስላችሁም”። 19 ሕዝቡ ግን ሳሙኤልን ለመስማት እምቢ አሉ፤ 20 ሳሙኤልንም፥ “አይሆንም፥ ንጉሣችን እንዲፈርድልን፥ በፊታችን እንዲሄድና ጦርነቶቻችንን እንዲዋጋልን፥ እንደ ሌሎች ሕዝቦች ሁሉ ለእኛም ንጉሥ ሊሆንልን ይገባል” አሉት። 21 ሳሙኤል የሕዝቡን ቃል ሁሉ በሰማ ጊዜ እርሱም በእግዚአብሔር ጆሮ ደግሞ ተናገረው። 22 እግዚአብሔርም ሳሙኤልን፥ “ቃላቸውን ታዘዝና ንጉሥ አድርግላቸው” አለው። ስለዚህ ሳሙኤል የእስራኤልን ሰዎች፥ “እያንዳንዱ ወደገዛ ከተማው ይሂድ” አላቸው።



1 Samuel 8:1

ነውረኛ ትርፍ ያሳድዱ ነበር

ጸሐፊው ሰው ወይም እንስሳ ከሳሙኤል ልጆች አምልጠው ይሮጡ የነበር ይመስል፣ የሳሙኤልም ልጆች ሰውና እንስሳ በተጨባጭ ያሳድዱ የነበሩ ይመስል፣ ሕዝቡ ለሳሙኤል ልጆች ስለሚሰጠው ገንዘብ ይናገራል፡፡ (ምትክ ቃል ተመልከት)

ፍርድን ያጣምሙ ነበር

ክፉ ለሚያደርጉ በማድላት ይፈርዳሉ

1 Samuel 8:4

በመንገድህ አይሄዱም

አንድ ሰው የሚኖርበት መንገድ እንደ ጎዳና ተገልጾአል፡፡ አት፡- አንተ የምታደርጋቸውን ነገሮች አያደርጉም ወይም አንተ ታደርገው እንደ ነበር ጽድቅ የሆነውን ነገር አያደርጉም ነበር፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

እንደ ሕዝቦች ሁሉ የሚፈርድልን ንጉሥ ሹምልን

ሊሆኑ የሚችል ትርጉሞች፣ 1) "እንዲፈርድልን የሕዝቦችን ሁሉ ነገሥታት የሚመስል ንጉሥ ሹምልን' ወይም 2) "የሕዝቦች ነገሥታት በሚፈርዱላቸው መንግድ የሚፈርድልን ንጉሥ ሹምልን'

የሚፈርድልን ንጉሥ ሹምልን

አለቆቹ በስህተት ንጉሡና ከእርሱም በኋላ ልጆቹ በጽድቅ ይገዛሉ ብለው አመኑ፡፡

1 Samuel 8:6

የሚፈርድልን ንጉሥ ሥጠን … ነገር ግን ሳሙኤልን አስከፋው

ሕዘቡ ምግባረ ብልሹ የሆኑ ልጆቹን አስውግዶ ሌሎች የታመኑ ፈራጆችን እንዲሾምላቸው ሳይሆን ሌሎች አገራት እንዳላቸው ዓይነት በላያቸው ላይ የሚገዛ ንጉሥ በመፈለጋቸው ሳሙኤል ደስተኛ አልሆነም፡፡

የሕዝቡን ቃል ስማ

ቢዘህ ስፍራ "ቃል' የሕዝቡን ፈቃድና ፍላጎት የሚያመልክት ምትክ ቃል ነው፡፡ (ምትክ ቃል ተመልከት)

ነገር ግን የተቃወሙት እኔ ነው

ሕዝቡ የተቃወሙት ምግባረ ብልሹ የሆኑትን ፈራጆች ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር ንጉሣቸው እንዳይሆን እየተቃወሙት እንደ ነበር እግዚአብሔር ያውቅ ነበር፡፡

1 Samuel 8:8

ከግብጽ አወጣኋቸው

ይህ ከብዙ ዓመታት በፊት እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከግብጽ ባርነት ነጻ ማውጣቱን ያመለክታል፡፡

አሁን ቃላቸውን ስማ

"አሁን እንድታደርግ የሚጠይቁህን አድርግ'

በጽኑ አስጠንቅቃቸው

ስታስጠነቅቃቸው የምር አድርገው

1 Samuel 8:10

ወጉ ይህ ነው … ይወስዳል

የንጉሥ ወግ መውሰድ ይሆናል፡፡ ይህ የሚወስዳቸውን ነገሮች ዝርዝር ይጀምራል፡፡

በእናንተ ላይ የሚነግሠው የንጉሥ ወግ ይህ ነው

ወግ የሚለው የነገር ስም በማሰሪያ አንቀጽነት ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "በላያችሁ የሚነግሠው ንጉሥ የሚያደርገው እንዲህ ነው' ወይም "በላያችሁ የሚነግሠው ንግሥ የሚሠራው እንዲህ ነው' (የነገር ስም ተመልከት)

ሰረገለኞቹ ያደርጋቸዋል

ወደ ጦርነት ሰረጋላ ያስነዳቸዋል

ፈረሰኞቹ ይሆናሉ

ወደ ጦርነት ፈረሶችን ይጋልባሉ

1 Samuel 8:13

አያያዥ አሳቦች

ሳሙኤል ንጉሥ የሚስዳቸውን ነገሮች መናገሩን ቀጠለ፡፡

ሽቶ ቀማሚዎች

ሰውነቱን የሚቀባው መልካም ሽታ ያለው ዘይት መሥራት

የወይራ እርሻ

የወይራ ዛፍ ማሳ

የእህላቸሁን አንድ አሥረኛ

እህላቸውን በአሥር እኩል ቦታ መክፈልና ከእነዚያ ክፍሎች አንዱን ለንጉሥ አለቆችና አገልጋዮች መስጠት ይኖርባቸዋል፡፡ (ክፍልፋይ ተመልከት)

የወይናችሁን አንድ አሥረኛ

በወይን እርሻቸው ያመረቱትን በአሥር እኩል ቦታ መክፈልና ከእነዚያ ክፍሎች አንዱን ለንጉሥ አለቆችና አገልጋዮች መስጠት ይኖርባቸዋል፡፡ (ክፍልፋይ ተመልከት)

አለቆች

እነዚህ የንጉሡ ሠራዊት አዛዦች ናቸው፡፡

1 Samuel 8:16

አያያዥ አሳቦች

ሳሙኤል ንጉሥ የሚስዳቸውን ነገሮች መናገሩን ቀጠለ፡፡

የመንጋችሁን አንድ አሥረኛ

መንጋቸውን በአሥር እኩል ቦታ መክፈልና ከእነዚያ ክፍሎች አንዱን ለንጉሥ አለቆችና አገልጋዮች መስጠት ይኖርባቸዋል፡፡ አንድ አሥረኛን በ1ሳሙኤል 8፡15 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት (ክፍልፋዮች ተመልከት)

ባሮቹ ትሆናላችሁ

"ባሮቹ እንደሆናችሁ ይሰማችኋል'

ትጮኻላችሁ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡-1)ከንጉሡ እንዲያድናቸው ሕዝቡ እግዚአብሔርን ይጠይቃሉ 2)የከፋ አገዛዙን አንዲያቆም ሕዝቡ ንጉሡን ይጠይቃሉ

1 Samuel 8:21

ለእግዚአብሔር ጆሮች ደገማቸው

በዚህ ስፍራ የእግዚአብሔር ጆሮች የሚለው እግዚአብሔርን ያመለክታል፡፡ ሕዝቡ ያሉትን ሁሉ በመድገም ሳሙኤል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ አት፡- ለእግዚአብሔር ደገማቸወ (ተለዋጭ ስም ተመልከት)

ቃላቸውን ስማ

"ቃላቸውን' የሚለው ምትክ ቃል የሕዝቡን ፈቃድ ያመለክታል፡፡ አት፡- "ሕዝቡን ታዘዝ' (ምትክ ቃል ተመልከት)

አንግሥላቸው

አንድን ሰው በላያቸው ላይ አንግሥላቸው፡፡ አንድን ሰው ንጉሥ ማድረግን በሚመለከት የተለመደ ቃል በቋንቋህ ካለ ተጠቀም፡፡

ወደ ከተማው ሄደ

"ወደ ቤት'


Chapter 9

1 ከብንያም ወገን ጽኑ ኃያል የሆነ አንድ ሰው ነበር። ስሙ ቂስ ሲሆን እርሱም የአቢኤል ልጅ፥ የጽሮር ልጅ፥ የብኮራት ልጅ፥ የብንያማዊው የአፌቅ ልጅ ነበር። 2 እርሱም ሳኦል የሚባል መልከ መልካም ወጣት ልጅ ነበረው። ከእርሱ የሚበልጥ መልከ መልካም ሰው በእስራኤል ሕዝብ መካከል አልነበረም። ከሕዝቡ ሁሉ ይልቅ ቁመቱ ረጅም ነበር። 3 የሳኦል አባት የቂስ ሴት አህዮች ጠፍተው ነበር። ስለዚህ ቂስ ልጁን ሳኦልን፥ “ከአገልጋዮቻችን አንዱን ውሰድ፤ ተነሥናም አህዮቹን ፈልግ” አለው። 4 ስለዚህ ሳኦል በኮረብታማው በኤፍሬም አገር በኩል አልፎ ወደ ሻሊሻ ምድር ሄደ፥ ነገር ግን አላገኟቸውም። ከዚያም በሻዕሊም ምድር በኩል አለፉ፥ ነገር ግን በዚያ አልነበሩም። ከዚያም በብንያማውያን ምድር በኩል አለፉ፥ ነገር ግን አላገኟቸውም። 5 ወደ ጹፍ ምድር በመጡ ጊዜ፥ ሳኦል ከእርሱ ጋር የነበረውን አገልጋዩን፥ "ና እንመለስ፥ አለበለዚያ አባቴ ስለ አህዮቹ ማሰቡን ትቶ ስለ እኛ መጨነቅ ይጀምራል" አለው። 6 ነገር ግን አገልጋዩ እንዲህ አለው፥ “ስማኝ፥ በዚህ ከተማ ውስጥ አንድ የእግዚአብሔር ሰው አለ። እርሱም የተከበረ ሰው ነው፤ የሚናገረው ነገር ሁሉ ይፈጸማል። ወደዚያ እንሂድ፤ በየትኛው አቅጣጫ መሄድ እንዳለብን ሊነግረን ይችል ይሆናል"። 7 ከዚያም ሳኦል አገልጋዩን፥ "ታዲያ ወደ እርሱ የምንሄድ ከሆነ ለዚያ ሰው ምን ልንሰጠው እንችላለን? እንጀራው ከከረጢታችን አልቋል፥ ለእግዚአብሔር ሰው የምናቀርበው ምንም ስጦታ የለንም። ምን አለን?"አለው። 8 አገልጋዩም ለሳኦል፥ "ይኸውና፥ የሰቅል ጥሬ ብር አንድ አራተኛው አለኝ፥ በየትኛው አቅጣጫ መሄድ እንዳለብን እንዲነግረን ለእግዚአብሔር ሰው እሰጠዋለሁ" ሲል መለሰለት። 9 (ቀደም ሲል በእስራኤል ውስጥ፥ አንድ ሰው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለመጠየቅ በሚሄድበት ጊዜ፥ "ኑ፥ ወደ ባለ ራዕዩ እንሂድ" ይል ነበር። የዛሬው ነቢይ ቀደም ሲል ባለ ራዕይ ተብሎ ይጠራ 10 ነበር።)ከዚያም ሳኦል አገልጋዩን፥”መልካም ብለሃል። ና፥ እንሂድ“ አለው። ስለዚህ የእግዚአብሔር ሰው ወደነበረበት ከተማ ሄዱ። 11 ኮረብታው ላይ ወዳለው ከተማ በመውጣት ላይ እያሉ ወጣት ሴቶች ውሃ ለመቅዳት ሲወጡ አገኟቸው፤ ሳኦልና አገልጋዩም፥”ባለ ራዕዩ በዚህ አለ? “ በማለት ጠየቋቸው። 12 እነርሱም እንዲህ በማለት መለሱላቸው፥ "አዎን፤ ተመልከቱ፥ እንዲያውም ከፊታችሁ እየቀደመ ነው። ዛሬ ሕዝቡ በኮረብታው ራስ ላይ ስለሚሠዉ ወደ ከተማው ይመጣልና ፍጠኑ። 13 ወደ ከተማው እንደገባችሁ ለመብላት ወደ ኮረብታው ራስ ከመውጣቱ በፊት ታገኙታላችሁ። መሥዋዕቱን የሚባርከው እርሱ ስለሆነ፥ እርሱ ከመምጣቱ በፊት ሕዝቡ አይበሉም፤ ከዚያ በኋላም የተጋበዙት ይበላሉ። ወዲያውኑ ታገኙታላችሁና አሁን ወደ ላይ ውጡ።” 14 ስለዚህ ወደ ላይ ወደ ከተማው ወጡ። ወደ ከተማይቱ በመግባት ላይ እያሉም ሳሙኤል ወደ ኮረብታው ራስ ለመውጣት በእነርሱ አቅጣጫ ሲመጣ አዩት። 15 ሳኦል ከመምጣቱ ከአንድ ቀን በፊት እግዚአብሔር ለሳሙኤል እንዲህ ሲል ገልጦለት ነበር፥ 16 “ነገ በዚህ ሰዓት ከብንያም ምድር አንድ ሰው እልክልሃለሁ፥ በሕዝቤ በእስራኤል ላይ መስፍን እንዲሆን ትቀባዋለህ። እርሱም ሕዝቤን ከፍልስጥኤማውያን እጅ ያድናቸዋል። እርዳታ በመፈለግ መጮኻቸው ወደ እኔ ደርሷልና ሕዝቤን በርኅራኄ ተመልክቻለሁ።” 17 ሳሙኤል ሳኦልን ባየው ጊዜ፥ እግዚአብሔር እንዲህ አለው፥”ስለ እርሱ የነገርኩህ ሰው ይህ ነው! ሕዝቤን የሚገዛው ሰው እርሱ ነው።“ 18 ከዚያም ሳኦል በበሩ አጠገብ ወደ ሳሙኤል ቀረብ ብሎ፥”የባለ ራዕዩ ቤት የት እንደሆነ ንገረኝ“ አለው። 19 ሳሙኤልም ለሳኦል እንዲህ በማለት መለሰለት፥”ባለ ራዕዩ እኔ ነኝ። ከእኔ በፊት ቀድማችሁ ወደ ኮረብታው ራስ ውጡ፥ ዛሬ ከእኔ ጋር ትበላላችሁና። ነገ ጠዋት በአዕምሮህ ያለውን ነገር ሁሉ እነግርህና አሰናብትሃለሁ። 20 ከሦስት ቀን በፊት ጠፍተው የነበሩት አህዮች ተገኝተዋልና ስለ እነርሱ አታስብ። የእስራኤል ሁሉ ምኞት የተቀመጠው በማን ላይ ነው? በአንተና በአባትህ ቤት ሁሉ ላይ አይደለም? “ 21 ሳኦልም፥ "ከእስራኤል ነገዶች ትንሹ የሆነው ብንያማዊ አይደለሁም? ጎሳዬስ ከብንያም ነገድ ጎሳዎች ሁሉ የመጨረሻው አይደለም? ታዲያ እንዲህ ባለ ሁኔታ ለምን ትናገረኛለህ?"ሲል መለሰለት። 22 ከዚያም ሳሙኤል ሳኦልንና አገልጋዩን ወደ አዳራሹ አስገብቶ ሠላሳ ከሚያህሉ ከተጋበዙት ሰዎች ከፍ ባለው ስፍራ ላይ አስቀመጣቸው። 23 ሳሙኤልም ወጥ ሠሪውን፥ "'ለብቻ አስቀምጠው' ብዬ የሰጠሁህን ድርሻ አምጣው" አለው። 24 ወጥ ሠሪውም በመሥዋዕቱ ጊዜ ያነሣውን ጭኑንና ከእርሱ ጋር ያለውን አምጥቶ በሳኦል ፊት አኖረው። ከዚያም ሳሙኤል፥ "የተቀመጠልህን ተመልከት! ለአንተ እስከተወሰነው ሰዓት ድረስ የቆየልህ ነውና ብላው። አሁን 'ሕዝቡን ጋብዣለሁ' ማለት ትችላለህ" አለው። ስለዚህ በዚያን ቀን ሳኦል ከሳሙኤል ጋር በላ። 25 ከኮረብታው ራስ ወደ ከተማው በወረዱ ጊዜ፥ በቤቱ የጣሪያ ወለል ላይ ሳሙኤል ከሳኦል ጋር ተነጋገረ። 26 ከዚያም በነጋ ጊዜ ሳሙኤል በጣሪያው ወለል ላይ ሳኦልን ተጣርቶ፥ "መንገድህን እንድትሄድ አሰናብትህ ዘንድ ተነሥ" አለው። ስለዚህ ሳኦል ተነሣ፥ እርሱና ሳሙኤል ሁለቱም ወደ ጎዳናው ሄዱ። 27 ወደ ከተማው ዳርቻ በመሄድ ላይ እያሉ፥ ሳሙኤል ሳኦልን፥ "አገልጋዩ ከፊታችን ቀድሞ እንዲሄድ ንገረው፥ (እርሱም ቀድሞ ሄደ) አንተ ግን የእግዚአብሔርን መልዕክት እንዳስታውቅህ እዚህ ጥቂት መቆየት አለብህ" አለው።



1 Samuel 9:1

አጠቃላይ መረጃ

በእነዚህ ቁጥሮች ጸሐፊው የሚሰጠው የታሪካዊ ዳራ መረጃ ለአንባቢ መናገር የሚቻልበት ሌላ መንገድ በቋንቋህ ካለ እዚህ ጋ መጠቀም ትችላለህ፡፡ (ታሪካዊ ዳራ መረጃ ተመልከት)

ተሰሚነት ያለው ሰው

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) ባላጠጋ ሰው ነበር 2) የመሣፍንት ዘር ነበር 3) ኃያልና ጎበዝ ሰው ነበር

ቂስ … አቢኢል … ጽሮር … ብኮራት … አፌቅ

እነዚህ የሳኦል የትውልድ ሐረግ ሰዎች ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ብንያማዊ

ብንያማዊ ከብንያም ነገድ የሆነ ሰው ነው

መልከ መልካም

ሲታይ መልካም የሆነ

ከሕዝቡም ሁሉ ይልቅ ከትከሻውና ከዚያም በላይ ቁመቱ ዘለግ ያለ ነበረ

በእስራኤል የነበሩ ሌሎች ረጃጅም ሰዎች ትከሻው ጋ አይደርሱም ነበር፡፡

1 Samuel 9:3

አሁን

ጸሐፊው የታሪካዊ ዳራ መረጃ መስጠቱን ጨርሶ (1ሳሙኤል 9፡1-2) የታሪኩን አዲስ ዋና ክፍል ይጀምራል፡፡

ተነሣና ሂድ

"እያደረግህ ያለውን አቁምና ሂድ'

ተራራማው የኤፍሬም አገር … የሻሊሻ ምድር … የሻዕሊ ምድር … የብንያም ምድር

እነዚህ ሁሉ በእስራኤል ውስጥ ያሉ አካባቢዎች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

አላገኙአቸውም … አልነበሩም … አላገኙአቸውምም

ሁሉም አህዮችን የሚያመልክቱ ናቸው፡፡

1 Samuel 9:5

የጹፍ ምድር

ይህ ከኢየሩሳሌም በስተሰሜን የሚገኝ በእስራኤል ውስጥ ያለ አካባቢ ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

የእግዚአብሔር ሰው

ይህ ሐረግ በአብዛኛው የእግዚአብሔር ነቢይ ማለት ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 2፡27 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ አት፡- "ከእግዚአብሔር ቃል ሰምቶ የሚናገር ሰው'

በጉዟችን የትኛውን መንገድ መሄድ እንዳለብን

"አህዮቹን ለማግኘት የትኛውን መንገድ መሄድ አለብን?'

1 Samuel 9:7

ለሰውዬው ምን እናመጣለታለን

ሥጦታ መሥጠት ለእግዚአብሔር ሰው የአክብሮት ምልክት ነው፡፡

የእግዚአብሔር ሰው

ይህ ሐረግ በአብዛኛው የእግዚአብሔር ነቢይ ማለት ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 2፡27 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ አት፡- "ከእግዚአብሔር ቃል ሰምቶ የሚናገር ሰው'

የሰቅል ሩብ

"የሰቅል አንድ አራተኛ'፡፡ ሰቅል በብሉይ ኪዳን አገልግሎት ይሰጥ የነበረ የገንዘብ ዓይነት ነው፡፡ (የመጽሐፍ ቅዱስ ገንዘቦችና ክፍልፋዮች ተመልከት)

1 Samuel 9:9

ቀድሞ በእስራኤል … ባለ ራእይ

ይህ በዕብራዊ ጸሐፊ የተጨመረ ባሕላዊ መረጃ ነው፡፡ ይህንን መረጃ በዚህ ስፍራ ማስቀመጥ በቋንቋህ የተለመደ ካልሆነ ወደ ቁጥር 11 መጨረሻ ሊወሰድ ይችላል፡፡ (ታሪካዊ ዳራ መረጃ ተመልከት)

ዛሬ ነቢይ የሚባለው ቀድሞ ባለ ራእይ ይባል ነበር

"ባለ ራእይ የሚለው ዛሬ ነቢይ ለሚባለው የጥንት መጠሪያ ነበር፡፡'

1 Samuel 9:12

ሕዝቡ ዛሬ መሥዋዕት ያቀርባሉ

ይህ በመገናኛው ድንኳን መከናወን ያለበት የኃጢአት መሥዋዕት ሳይሆን፣ የበዓል ወይም የበኩራት መሥዋዕቶችን የሚመለክት ይመስላል፡፡

1 Samuel 9:14

ወደ ኮረብታው መስገጃ መውጣት

ይህ ለእግዚአብሔር መሥዋዕትና ቁርባን ለማቅርብ ሕዝቡ ቅዱስ ቦታ ብለው የሰየሙት ስፍራ ነው፡፡ ጸሐፊው በከተማይቱ ዙሪያ ካለው ቅጥር ውጪ ይገኝ እንደ ነበር ይጽፋል፡፡

1 Samuel 9:15

አጠቃላይ መረጃ

ጸሐፊው ታሪኩን መናገር ያቆምና አንባቢው በመቀጠል የሚሆነውን እንዲረዳ የታሪካዊ ዳራ መረጃ ይሰጣል፡፡ (ታሪካዊ ዳራ መረጃ ተመልከት)

ልዑል ይሆን ዘንድ ትቀባዋለህ

በዚህ ስፍራ ልዑል የሚለው ቃል ንጉሥ በሚለው ፈንታ ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ የእስራኤል ንጉሥ እንዲሆን እግዚአብሔር የመረጠው ሰው ይህ ነው፡፡ (የማያስደስትን ቃል በሌላ ቃል መጠቀም ተመልከት)

የብንያም ምድር

"ከብንያም ነገድ የሆኑ ሰዎች የሚኖሩበት ምድር'

ከፍልስጥኤማውያን እጅ

በዚህ ስፍራ እጅ የሚለው ቃል ቁጥጥር ለሚለው ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "ከፍልስጥኤማውያን ቁጥጥር' ወይም "ከእንግዲህ ወዲያ ፍልስጥኤማውያን አይቆጣጠሩአቸውም'

ሕዝቤን በሐዘኔታ ተመልክቼአለሁና

"ሕዝቤ መከራ እያዩ ናቸው እኔም ልረዳቸው እፈልጋለሁ'

1 Samuel 9:17

እግዚአብሔር አለው

"እግዚአብሔር ሳሙኤልን አለው'

ባለ ራእዩ

"የእግዚአብሔር ነቢይ'

1 Samuel 9:20

የእስራኤል ምኞት ለማን ነው? ለአንተና ለአባትህ ቤት አይደለምን?

እነዚህ ጥያቄዎች ሳኦል እስራኤል የሚፈልጉት እግዚአብሔር ንጉሥ እንዲሆን የወደደው ሰው ለመሆኑ የጥልቅ መረዳት ማሳያ ናቸው፡፡ ጥያቄዎቹ በገላጭ አባባል ሊገለጹ ይችላሉ፡፡ አት፡- "የእስራኤል ምኞት ሁሉ ያረፈው በአንተ ላይ እንደሆነ ልታውቅ ይገባሃል፡፡ ዓይናቸውን በአንተና በአባትህ ቤት ላይ ጥለዋል፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄዎች ተመልከት)

እኔ ከእስራኤል … ብንያማዊ አይደለሁምን? ከብኒያም ነገድ … አይደለሁምን? እንዲህስ ያለውን ነገር ለምን ነገርኸኝ?

ብንያም በእስራኤል ትንሹ ነገድና ሌሎች እስራኤላውያን እንደማይጠቅም ነገድ የሚቆጥሩት ስለሆነ ሳኦል ግርምቱን እየገለጠ ነው፡፡ በተጨማሪም፣ ሳኦል አባል የሆነበትን ጎሳ ብንያማውያን እንደማይጠቅም ይቆጥሩት ነበር፡፡ እነዚህ ጥያቄዎች በገላጭ አባባል ሊተረጎሙ ይችላሉ፡፡ አት፡- እኔ ከነገዶች ሁሉ አስፈለጊነቱ የመጨረሻ ዝቅተኛ ከሆነው ከብንያም ነገድ ነኝ፡፡ ጎሳዬም በነገዳችን አስፈላጊነቱ የመጨረሻ ዝቅተኛ ጎሳ ነው፡፡ የእስራኤል ሕዝብ እኔንና ቤተሰቤን አስፈላጊ ነገር እንድናደርግ እንደሚፈለጉን ለምን እንደምትነግረኝ ልረዳ አልቻልኩም፡፡ (አሳብ ገላጭ ጥያቄዎች ተመልከት)

1 Samuel 9:22

አዳራሽ

መሥዋዕት በሚያቀርቡበት ስፍራ በአቅራቢያው ሰዎች በአንድነት የሚመገቡበት ትልቅ ሕንፃ እንደነበር አንባቢው እንደሚያውቅ ጸሐፊው ይገምታል፡፡

ራስ ስፍራ

የክብር መቀመጫ

ሠላሣ ሰዎች

"30 ሰዎች' (ቁጥሮች ተመልከት)

1 Samuel 9:23

በእርሱ ላይ የነበረውን

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) ሳኦል ከስጋው ጋር ሊበላው የነበረ ሌላ ምግብ ወይም 2) የወይፈኑ ሌሎች ክፍሎች

ሳሙኤልም አለ

በመጀመሪያው ቋንቋ ተናጋሪው ማን እንደሆነ ግልጽ አይደለም፡፡ ወጥ ቤቱም ለሳኦል እየተናገረ ሊሆን ይችላል፡፡ አት፡- "ወጥ ቤቱም አለ'

1 Samuel 9:25

በሰገነቱ ላይ

ይህ ለቤተሰብና ለእንግዶች ለመብላት፣ ለመጎብኘትና ለመተኛት የተለመደ ቦታ ነው፡፡ በምሽትና በሌሊት ከቤቱ ውስጠኛ ክፍል ይልቅ የመቀዝቀዝ ሁኔታ ይታይበታል፡፡

ሳሙኤል ሳኦልን ከሰገነቱ ላይ ጠራና አለው

ሳኦል በሰገነቱ ላይ ያደርግ የነበረው ግልጽ ሊደረግ ይቻላል፡፡ አት፡- "ሳኦል በሰገነቱ ላይ ተኝቶ ሳለ፣ ሳሙኤል ጠራውና አለ' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 9:27

በፊታችን እንዲያለፍ "–ብላቴናውም አለፈ –' አንተ ቁም

እነዚህን ቃላት ሁሉ ሳሙኤል ተናግሮ ሊሆን ይችላል፡፡ አት፡- "ከፊታችን ይለፍ፣ ከፊታችንም ሲያለፍ፣ አንተ ቆይ'


Chapter 10

1 ከዚያም ሳሙኤል የዘይቱን ጠርሙስ ወስዶ በሳኦል ራስ ላይ አፈሰሰው፤ ሳመውም። እርሱም እንዲህ አለው፥ "በርስቱ ላይ ገዢ እንድትሆን እግዚአብሔር ቀብቶሃል፤ 2 ዛሬ ከእኔ ተለይተህ ስትሄድ፥ የብንያም ወሰን በሆነው በጼልጻህ፥ በራሔል መቃብር አጠገብ ሁለት ሰዎች ታገኛለህ። እነርሱም፥ 'ስትፈልጋቸው የነበሩት አህዮች ተገኝተዋል። አሁን አባትህ ስለ አህዮቹ ማሰቡን ትቶ፥ "ስለ ልጄ ምን ባደርግ ይሻለኛል?" በማለት ተጨንቋል“ ይሉሃል። 3 ከዚያ አልፈህ ትሄድና በታቦር ወደሚገኘው ወደ በሉጥ ዛፍ ትመጣለህ። ወደ ቤቴል፥ ወደ እግዚአብሔር የሚሄዱ አንደኛው ሦስት የፍየል ጠቦቶች ይዞ፥ ሌላኛው ሦስት ዳቦ ተሸክሞ፥ ሌላኛው ደግሞ ወይን ጠጅ የተሞላ አንድ አቁማዳ ተሸክሞ ሦስት ሰዎች ይገናኙሃል። 4 ሰላምታ ከሰጡህ በኋላ ሁለት ዳቦ ይሰጡሃል፥ ከእጃቸውም ትቀበላቸዋለህ። 5 ከዚህ በኋላ የፍልስጥኤም የጦር ሠፈር ወዳለበት ወደ እግዚአብሔር ኮረብታ ትመጣለህ። ወደ ከተማው በምትደርስበት ጊዜ፥ አንድ የነቢያት ቡድን በፊታቸው መሰንቆ፥ ከበሮ፥ እምቢልታና በገና ይዘው ከተራራው ሲወርዱ ትገናኛቸዋለህ፤ እነርሱም ትንቢት ይናገራሉ። 6 የእግዚአብሔር መንፈስ በኃይል ይመጣብሃል፥ አንተም ከእነርሱ ጋር ትንቢት ትናገራለህ፥ እንደ ሌላ ሰው ሆነህም ትለወጣለህ። 7 እነዚህ ምልክቶች በሚፈጸሙልህ ጊዜ፥ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነውና እጅህ ያገኘውን ሁሉ አድርግ። 8 ቀድመኸኝ ወደ ጌልገላ ውረድ። ከዚያም የሚቃጠለውን መባ ለማቅረብና የሰላሙን መባ ለመሠዋት ወደ አንተ እወርዳለሁ። ወደ አንተ እስክመጣና ልታደርገው የሚገባህን እስከማሳይህ ድረስ ሰባት ቀን ቆይ።” 9 ሳኦል ከሳሙኤል ተለይቶ ለመሄድ ፊቱን ባዞረ ጊዜ እግዚአብሔር ሌላ ልብ ሰጠው። እነዚህ ምልክቶች ሁሉ በዚያው ቀን ተፈጸሙ። 10 እነርሱም ወደ ኮረብታው በመጡ ጊዜ፥ የነቢያት ቡድን ተገናኙት፥ የእግዚአብሔርም መንፈስ በኃይል መጣበት፥ ከእነርሱም ጋር ትንቢት ተናገረ። 11 ቀድሞ ያውቁት የነበሩት ሁሉ እርሱም ከነቢያት ጋር ትንቢት ሲናገር ባዩት ጊዜ፥ እርስ በእርሳቸው፥ “የቂስን ልጅ ምን ነካው? አሁን ሳኦል ከነቢያት አንዱ መሆኑ ነው?” ተባባሉ። 12 በዚያው ስፍራ የነበረ አንድ ሰው፥ “አባታቸው ማነው?” ሲል መለሰ። በዚህ ምክንያት፥ “ሳኦልም ከነቢያት አንዱ ነው?” የሚል ምሳሌአዊ አባባል የተለመደ ሆነ። 13 ትንቢት መናገሩን በጨረሰ ጊዜ ወደ ተራራው ራስ መጣ። 14 ከዚያም የሳኦል አጎት፥ እርሱንና አገልጋዩን፥ “የት ነበር የሄዳችሁት?” አላቸው። እርሱም፥ “አህዮቹን ለመፈለግ ነበር፤ ልናገኛቸው እንዳልቻልን ባየን ጊዜ ወደ ሳሙኤል ሄድን” ብሎ መለሰለት። 15 የሳኦልም አጎት፥ “ሳሙኤል የነገረህን እባክህ ንገረኝ" አለው። 16 ሳኦልም አጎቱን፥ "አህዮቹ መገኘታቸውን በግልጽ ነገረን" ብሎ መለሰለት። ሳሙኤል ነግሮት የነበረውን የንግሥና ጉዳይ ግን አልነገረውም። 17 ሳሙኤል ሕዝቡን በአንድነት በእግዚአብሔር ፊት ወደ ምጽጳ ጠራቸው። 18 እርሱም የእስራኤልን ሕዝብ እንዲህ አላቸው፥”የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር የሚለው ይህንን ነው፥ 'እስራኤልን ከግብፅ አወጣሁት፥ ከግብፃውያን እጅና ካስጨነቋችሁ መንግሥታት ሁሉ እጅ አዳንኋችሁ'። 19 ነገር ግን ዛሬ እናንተ ከመከራና ከጭንቃችሁ ሁሉ የሚያድናችሁን አምላካችሁን ተቃውማችኋል፤ እርሱንም፥ 'በላያችን ላይ ንጉሥ አንግሥልን' ብላችሁታል። አሁን በየነገዳችሁና በየጎሣችሁ ራሳችሁን በእግዚአብሔር ፊት አቅርቡ"። 20 ስለዚህ ሳሙኤል የእስራኤልን ነገዶች በሙሉ አቀረበ፥ የብንያም ነገድም ተመረጠ። 21 ከዚያም የብንያምን ነገድ በየጎሣቸው አቀረበ፤ የማጥሪ ጎሣም ተመረጠ፤ የቂስ ልጅ ሳኦልም ተመረጠ። ነገር ግን በፈለጉት ጊዜ ሊያገኙት አልቻሉም። 22 ከዚያም ሕዝቡ”ገና የሚመጣ ሌላ ሰው አለ? “ በማለት እግዚአብሔርን ተጨማሪ ጥያቄዎች ለመጠየቅ ፈለጉ። እግዚአብሔርም፥”ራሱን በዕቃዎቹ መካከል ደብቋል" በማለት መለሰላቸው። 23 ከዚያም ሮጠው ሄዱና ሳኦልን ከዚያ አመጡት። በሕዝቡ መካከል በቆመ ጊዜ፥ ከሕዝቡ ሁሉ ይልቅ ቁመቱ ረጅም ነበር። 24 ሳሙኤልም ሕዝቡን፥ "እግዚአብሔር የመረጠውን ይህንን ሰው ታዩታላችሁ? በሕዝቡ ሁሉ መካከል እንደ እርሱ ያለ የለም! “ አላቸው። ሕዝቡም ሁሉ፥”ንጉሥ ለዘላለም ይኑር! “ በማለት ጮኹ። 25 ከዚያም ሳሙኤል የንግሥናን ደንብና ልማዶች ለሕዝቡ ነገራቸው፥ በመጽሐፍ ጽፎም በእግዚአብሔር ፊት አስቀመጣቸው። ከዚያም ሳሙኤል እያንዳንዱ ወደ ገዛ መኖሪያው እንዲሄድ ሕዝቡን ሁሉ አሰናበተ። 26 ሳኦልም ደግሞ በጊብዓ ወደሚገኘው መኖሪያው ሄደ፥ እግዚአብሔር ልባቸውን የነካቸው አንዳንድ ኃያላን ሰዎችም ከእርሱ ጋር ሄዱ። 27 አንዳንድ የማይረቡ ሰዎች ግን፥”ይህ ሰው ሊያድነን እንዴት ይችላል? “ አሉ። እነዚህ ሰዎች ሳኦልን ናቁት፥ ምንም ዓይነት ስጦታዎችንም አላመጡለትም። ሳኦል ግን ዝም አለ።



1 Samuel 10:1

የዘይቱን ብርሌ ወስዶ በሳኦል ራስ ላይ አፈሰሰው

በእስራኤል ባሕል፣ አንድ ነቢይ በአንድ ሰው ራስ ላይ ዘይት ሲያፈስስ፣ ግለሰቡ ከአግዚአብሔር ዘንድ በረከት ይቀበላል፡፡

ብርሌ

ከተጠበሰ የሸክላ አፈር የሚሠራ ትንሽ መያዣ

በርስቱ ላይ አለቃ ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አልቀባህምን?

ሳሙኤል ለጥያቄው የሚሰጠውን መልስ ያውቃል፡፡ በእስራኤል ላይ ንጉሥ ይሆን ዘንድ እግዚአብሔር እንደመረጠው ሳኦልን እያሳሰበው ነው፡፡ አት፡- "በርስቱ ላይ አለቃ ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር በእርግጥ ቀብቶሃል፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ጼልጻህ

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

የልጄን ነገር እንዴት አደርጋልሁ?

አሁን የሳኦል አባት ስለ ሳኦል መጨነቅ ጀመረ ሊያገኘውም ፈለገ፡፡

1 Samuel 10:3

ታቦር

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

ከእጃቸው ተቀበል

እጆች ለግለሰቦች ተለዋጭ ስም ነው፡፡ "ከእነርሱ ውሰድ' ወይም "ተቀበል' (ተለዋጭ ስም ተመልከት)

1 Samuel 10:5

ከበሮ

የሚመታ የታምቡር ራስ የሚመስል ያለው እና ሲንቀጠቀጥ ድምጽ የሚሰጡ የብረት ቁራጮች በጎኑ ዙሪያ ያለው የሙዚቃ መሣሪያ ነው፡፡ (የማይታወቁትን መተርጎም ተመልከት)

የእግዚአብሔር መንፈስ በኃይል ይወርድብሃል

ይወርድባሃል የሚለው ቃል የእግዚአብሔር መንፈስ በሳኦል ላይ ተጽእኖ ያድርጋል ማለት ነው፡፡ በዚህ ስፍራ ሳኦልን እንዲተነብይና እንደ ሌላ ሰው እንዲከውን ያደርገዋል ማለት ነው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 10:7

እጅህ የምታገኘውን ሁሉ አድርግ

በዚህ ስፍራ ሳሙኤል ስለ ሳኦል እጆች ነገሮችን ለማግኘት እንደሚጥር ግለሰብ አድርጎ ይናገራል፡፡ አት፡- "ለማድረግ ትክክል እንደሆነ የምታስበውን ሁሉ አድርግ' (ግዑዝ ነገርን እንደ ሰው ማየትን ተመልከት)

1 Samuel 10:9

እግዙአብሔር ሌላ ልብ ሰጠው

እግዚብአብሔር ሳኦልን ቀድሞ ያስብበት ከነበረበት መንገድ በተለየ መንገድ እንዲያስብ አስቻለው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

የእግዚአብሔር መንፈስ በኃይል ወረደበት

ሳሙኤል የእግዚአብሔር መንፈስ ወደ ሳኦል እንደሚሮጥና እርሱንም ሙሉ ለሙሉ እንደሚቆጣጠር ግለሰብ አድርጎ ይናገራል፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 10፡6 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ አት፡- "የእግዚአብሔር መንፈስ ሙሉ ለሙሉ ተቆጣጠረው' (ግዑዝ ነገርን እንደ ሰው ማየትን ተመልከት)

1 Samuel 10:11

የቂስን ልጅ ያገኘው ምንድን ነው

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) ሕዝቡ መረጃ እየጠየቀ ነው 2) ሳኦል አስፈላጊ ሰው አይደለም የሚል ትርጉም ያለው አሳብ ገላጭ ጥያቄ ነው፡፡ አት፡- "ቂስ አስፈላጊ ሰው አይደለም፣ ልጁ ነቢይ ሆነ የሚለው እውነት ሊሆን አይችልም፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

የቂስ ልጅ

"ሳኦል የቂስ ልጅ'

አባታቸውስ ማን ነው

ይህ ሰው፣ ነቢይ መሆን የአንድ ሰው ወላጆች እነማን ከመሆናቸው ጋር የሚያያዝው ምንም ነገር እንደሌለ ሕዝቡን ለማሳሳብ አሳብ ገላጭ ጥያቄ ይጠቀማል፡፡ ይህ ጥያቄ በገላጭ አባባል ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "የእነዚህ የሌሎቹ ነቢያት ወላጆች እነማን መሆናቸው አስፈላጊ ነገር አይደለም፡፡ ቁም ነገሩ፣ በሚያስገርም ሁኔታ፣ ሳኦል የእግዚአብሔርን መልእክት መናገሩ ነው፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄዎች ተመልከት)

ስለዚህም፡- "ሳኦል ደግሞ ከነቢያት ወገን ነውን?' የሚል አባባል ሆነ

ይህ በእስራኤላውያን መካከል ምሳሌ ሆነ፡፡ አንድ ሰው ከዚያ በፊት አድርጎት የማያውቀውን ነገር ሳይታሰብ አድርጉት ሲገኝ አድናቆትን ለመግለጽ ሰዎች በግልጽ ይህን ይላሉ፡፡ አት፡- "ሰዎች አንዳንድ ዘገባዎችን ማመን ባቃታቸው ጊዜ፣ ከዚያም የተነሳ፣ ለሳኦል ስለሆነው አሰቡና እንዲህ አሉ፣ ‘በውኑ ሳኦል ከነቢያት አንዱ ነውን?'' (ምሳሌዎችንና እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 10:14

ከዚያም የሰኦል አጎት እንዲህ አለው

"ከዚያም የሳኦል የአባቱ ወንድም እንዲህ አለው'

የመንግሥቱን ነገር በሚመለከት አልነገረውም

"እግዚአብሔር የእስራኤል ንጉሥ እንዲሆን እንደሾመው ሳኦል ለአጎቱ አልነገረውም'

1 Samuel 10:17

እስራኤልን ከግብጽ አወጣሁ

እስራኤል የሚለው ስም ለእስራኤል ሕዝብ ምትክ ስም ነው፡፡ አት፡- "የእስራኤልን ሕዝብ ከግብጽ አወጣሁ' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ዛሬ

ሳሙኤል ፀሐይ ለመጨረሻ ከጠለቀችበት አንስቶ ያለውን ጊዜ ብቻ ሳይሆን፣ እስራኤል እግዚአብሔርን መቃወም ከጀመሩበት አንስቶ ስላለው ጊዜ ይናገራል፡፡

የግብጻውያን እጅ … የመንግሥታት ሁሉ እጅ

እጅ የሚለው ቃል ለኃይል ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "የግብጻውያን ኃይል … የመንግሥታት ሁሉ ኃይል'

ንጉሥ አንግሥልን

"የሚገዛንን ንጉሥ ስጠን'

በየነገዳችሁና በየወገናችሁ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር አቅርቡ

"በየነገዳችሁና በየወገናችሁ በአንድ ተሰበሰቡና በእግዚአብሔር ፊት ለመቆም ኑ'

1 Samuel 10:20

የብንያም ነገድ ተመረጠ … የማጥሪን ወገን ተመረጠ … የቂስ ልጅ ሳኦል ተመረጠ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊተረጎም ይችላል፡፡ እግዚአብሔር የመረጠውን ሕዝቡ ያወቀበት መንግድ ብሎ አለመተረጎም እጅግ የተሻለ ነው፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር የብንያምን ነገደ መረጠ … እግዚአብሔር የማጥሪንን ወገን መረጠ … እግዚአብሔር የቂስን ልጅ ሳኦልን መረጠ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

1 Samuel 10:22

ከሕዝቡም ሁሉ ይልቅ ከትከሻውና ከዚያም በላይ ቁመቱ ዘለግ ያለ ነበረ

በእስራኤል የነበሩ ሌሎች ረጃጅም ሰዎች ትከሻው ጋ አይደርሱም ነበር፡፡ ይህን በ1ሳሙኤል 9፡2 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

1 Samuel 10:25

የንግሥና ወጎችና መመሪያዎች

ንግሥና የሚለው የነገር ስም በመጠሪያ ሐረግነት ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "ንጉሥ ሊከተላቸው የሚያስፈልጉ ወጎችና መመሪያዎች' (የነገር ስም ተመልከት)

1 Samuel 10:26

እግዚአብሔር ልባቸውን የነካ

የእግዚአብሔር የሰውን ልብ መንካት የእግዚአብሔር በአእምሮአቸው ውስጥ አንድን ነገር ማስቀመጥ ወይም አንድን ነገር እንዲያደርጉ ማንቀሳቀስ የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር አስተሳሰባቸውን ስለቀየረ ከሳኦል ጋር ለመሄድ የፈለጉ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ይህ ሰው እንዴት ያድነናል?

ይህ ማሽሟጠጥን ለመግለጽ ጥቅም ላይ የሚውል አሳብ ገላጭ ጥያቄ ነው፡፡ አት፡- "ይህ ሰው ሊያድነን ኃይል የለውም፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ናቁት

እጅግ አልወደዱትም ወይም ናቁት


Chapter 11

1 አሞናዊው ናዖስ ሄዶ ኢያቢስ ገለዓድን ከበባት። የኢያቢስ ሰዎች ሁሉ ናዖስን፥ "ከእኛ ጋር ቃል ኪዳን አድርግ፥ እኛም እናገለግልሃለን" አሉት። 2 አሞናዊው ናዖስም፥ "የሁላችሁንም ቀኝ ዐይኖቻችሁን በማውጣት በመላው እስራኤል ላይ ኃፍረትን አመጣለሁ፥ በዚህ ቅድመ ሁኔታ ከእናንተ ጋር ቃል ኪዳን አደርጋለሁ" ብሎ መለሰላቸው። 3 የኢያቢስ ሽማግሌዎችም፥ "ወደ እስራኤል ወገኖች ሁሉ መልዕክተኞችን እንድንልክ ለሰባት ቀናት ታገሰን። ከዚያም የሚያድነን አንድም ባይኖር ለአንተ እንገዛለን" በማለት መለሱለት። 4 መልዕክተኞቹም ሳኦል ወደሚኖርበት ወደ ጊብዓ መጥተው የሆነውን ነገር ለሕዝቡ ነገሯቸው። ሕዝቡም ሁሉ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ። 5 በዚህ ጊዜ ሳኦል ከእርሻ በሬዎቹን እየነዳ መጣ። ሳኦልም፥ "ሕዝቡ ምን ሆኖ ነው የሚያለቅሰው?" አለ። እነርሱም የኢያቢስ ሰዎች ያሉትን ለሳኦል ነገሩት። 6 ሳኦል የነገሩትን በሰማ ጊዜ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ በኃይል መጣበት፥ እጅግም ተቆጣ። 7 የበሬዎቹን ቀንበር ወስዶ ፈለጣቸውና ወደ እስራኤል ወሰኖች ሁሉ በመልዕክተኞች እጅ ላከው። እርሱም፥ "ሳኦልንና ሳሙኤልን ተከትሎ በማይመጣው ሁሉ በበሬዎቹ ላይ እንዲህ ይደረግበታል" አለ። ከዚያም ከእግዚአብሔር ታላቅ ፍርሃት በሕዝቡ ላይ ወደቀ፥ እንደ አንድ ሰው ሆነው ተሰብስበው መጡ። 8 ቤዜቅ በተባለ ስፍራ በሰበሰባቸው ጊዜ፥ የእስራኤል ሰዎች ሦስት መቶ ሺህ፥ የይሁዳም ሰዎች ሠላሳ ሺህ ነበሩ። 9 እነርሱም ለመጡት መልዕክተኞች፥ "ለኢያቢስ ገለዓድ ሰዎች፥ 'ነገ ፀሐይ ሞቅ በሚልበት ሰዓት እንታደጋችኋለን' ብላችሁ ንገሯቸው" አሏቸው። መልዕክተኞቹ ሄደው ለኢያቢስ ሰዎች ነገሯቸው፥ እነርሱም እጅግ ደስ አላቸው። 10 ከዚያም የኢያቢስ ሰዎች ናዖስን፥”ነገ እንገዛልሃለን፥ አንተም ደስ የሚያሰኝህን ልታደርግብን ትችላለህ“ አሉት። 11 በቀጣዩ ቀን ሳኦል ሕዝቡን በሦስት ቡድን ከፈላቸው። ሊነጋጋ ሲል ወደ ጦር ሠፈሩ መካከል መጡ፥ አሞናውያንንም አጠቁ፥ ቀኑ እስኪሞቅ ድረስም አሸነፏቸው። በሕይወት የተረፉትም ከእነርሱ ሁለቱ አንድ ላይ ሆነው እስከማይታዩ ድረስ ተበታተኑ። 12 በዚያን ጊዜ ሕዝቡ ሳሙኤልን፥ "'ሳኦል በእኛ ላይ እንዴት ይነግሣል?' ያለው ማን ነበር? እንድንገድላቸው ሰዎቹ ይምጡልን" አሉት። 13 ነገር ግን ሳኦል፥ "ዛሬ እግዚአብሔር እስራኤልን ታድጎታልና በዚህ ቀን ማንም መገደል የለበትም" አላቸው። 14 ሳሙኤልም ሕዝቡን፥ "ኑ፥ ወደ ጌልገላ እንሂድና በዚያ መንግሥቱን እናድስ" አላቸው። 15 ስለዚህ ሕዝቡ ሁሉ ወደ ጌልገላ ሄደው በእግዚአብሔር ፊት በጌልገላ ሳኦልን አነገሡት። በዚያም በእግዚአብሔር ፊት የሰላምን መባ ሠዉ፥ ሳኦልና የእስራኤል ሰዎችም ሁሉ እጅግ ደስ አላቸው።



1 Samuel 11:1

ናዖስ

ይህ ሰው የአብርሃም የወንድም ወይም የእኅት ልጅ የሎጥ ትውልድ የሆነ አሞናዊ ነው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)፡፡

ኢያቢስ ገለዓድ

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

አወጣለሁ

"ቆርጬ አወጣለሁ' ወይም "ጎትቼ አወጣለሁ'

ውርደት አመጣባችኋለሁ

"ውርደት አለብሳችኋለሁ' ወይም "አሳፋሪ ስም አለብሳችኋለሁ'

1 Samuel 11:3

ሰባት ቀናት

"7 ቀናት' (ቁጥሮች ተመልከት)

1 Samuel 11:4

ጊብዓ

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 11:6

የእግዚአብሔር መንፈስ በኃይል ወረደበት

ወረደበት የሚለው ቃል የእግዚአብሔር መንፈስ በሳኦል ላይ ተጽእኖ ያድርጋል ማለት ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ እንደ ንጉሣቸው ሕዝቡ በፍርሃት እንዲያከብሩትና ሠራዊቱን እንዲቀላቀሉ እንዲያደርግ ሳኦልን አስችሎታል፡፡ 1ሳሙኤል 10፡6ን እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

ተከትሎ የማይወጣ

ናዖስንና አሞናውያንን ለመወጋት የእስራኤል ሰዎች ሁሉ እንዲመጡ ሳዖል ጥሪ እያስተላለፈ ነበር፡፡

ከዚያም የእግዚአብሔር ድንጋጤ በሕዝቡ ላይ ወደቀ

እንደ ንጉሣቸው ሳኦልን በፍርሃት እንዲያከብሩት እግዚአብሔር ሕዘቡን አስቻለ፡፡ በውጤቱም ሰዎቹ ከሳኦል ጋር በቤዜቅ በአንድነት ተሰበሰቡ፡፡

ቤዜቅ

ይህ በኢያቢስ ገለዓድ አቅራቢያ የምትገኝ ከተማ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

የእስራኤል ሰዎች ሦሥት መቶ ሺህ፣ የይሁዳም ሰዎች ሠላሣ ሺህ ነበሩ

"የእስራኤል ሰዎች 300,000፣ የይሁዳም ሰዎች 30,000 ነበሩ' (ቁጥሮች ተመልከት)

1 Samuel 11:9

መልእክተኞቹን አሉአቸው

"አሉአቸው' የሚለው ሳሙኤልንና ሳሙኤልን ያመለክታል፡፡

ፀሐይ በሞቀች ጊዜ

"ከቀኑ እጅግ ሞቃት ከሆነው ክፍል በፊት' ወይም "ከቀትር በፊት'

ኢያቢስ ገለዓድ … ኢያቢስ

እነዚህ የቦታዎች ስሞች ናቸው፡፡ በ1ሳሙኤል 11፡1 እንዴት እንደተረጎምሃቸው ተመልከት፡፡

ናዖስ

ይህ የንጉሥ ስም ነው፡፡ ይህንን ስም በ1ሳሙኤል 11፡1 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

1 Samuel 11:11

በነጋውም

ይህ ከንጋት በፊት አብዛኛው ሕዝብ ገና በሰፈሩ ተኝቶ የነበረበት ጊዜ ነው፡፡

1 Samuel 11:14

ሳኦልን በእግዚአብሔር ፊት አነገሡት

"እግዚአብሔር እያየ ሳኦልን አነገሡት'

በዚያም በእግዚአብሔር ፊት የሰላም መሥዋእት አቀረቡ

ከአሮን ወይም ከሌዊ ቤት ባይሆንም እንኳን መሥዋዕት ማቅረብ የሳሙኤል የእግዚአብሔር አገልግሎት ክፍል ነው፡፡


Chapter 12

1 ሳሙኤል እስራኤላውያንን በሙሉ እንዲህ አላቸው፥”የነገራችሁኝን በሙሉ ሰምቻችኋለሁ፥ ንጉሥንም በላያችሁ ላይ አንግሼላችኋለሁ። 2 አሁንም፥ በፊታችሁ የሚሄድላችሁ ንጉሥ ይኸውላችሁ፤ እኔ አርጅቻለሁ፥ ጸጉሬም ሸብቷል፤ ልጆቼም ከእናንተ ጋር ናቸው። ከልጅነቴ ጀምሮ እስካሁን ድረስ በፊታችሁ ኖሬአለሁ። 3 ይኸው በፊታችሁ ነኝ፤ በእግዚአብሔርና እርሱ በቀባው ፊት መስክሩብኝ። የማንን በሬ ወስጃለሁ? የማንንስ አህያ ወስጃለሁ? ማንን አታለልሁ? በማንስ ላይ ግፍ ሠራሁ? ዓይኖቼን ለማሳወር ከማን እጅ ጉቦ ተቀበልሁ? መስክሩብኝና እመልስላችኋለሁ።“ 4 እነርሱም፥”አላታለልከንም፥ ግፍም አልሠራህብንም ወይም ከማንም እጅ ምንም ነገር አልሰረቅህም“ አሉ። 5 እርሱም፥”በእጄ ላይ ምንም እንዳላገኛችሁ ዛሬ እግዚአብሔር በእናንተ ላይ ምስክር ነው፥ እርሱ የቀባውም ምስክር ነው“ አላቸው። እነርሱም፥”እግዚአብሔር ምስክር ነው“ ብለው መለሱ። 6 ሳሙኤልም ሕዝቡን፥”ሙሴንና አሮንን የመረጣቸው፥ አባቶቻችሁንም ከግብፅ ምድር ያወጣቸው እግዚአብሔር ነው። 7 አሁን እንግዲህ፥ እግዚአብሔር ለእናንተና ለአባቶቻችሁ ስለ ሠራላችሁ የጽድቅ ሥራ ሁሉ እንድሟገታችሁ በእግዚአብሔር ፊት ራሳችሁን አቅርቡ። 8 ያዕቆብ ወደ ግብፅ በመጣ ጊዜ አባቶቻችሁ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ። እግዚአብሔር፥ ከግብፅ ምድር እየመሩ አውጥተው በዚህ ስፍራ እንዲቀመጡ ያደረጓቸውን ሙሴንና አሮንን ላከ። 9 እነርሱ ግን አምላካቸውን እግዚአብሔርን ረሱ፤ እርሱም የሐጾር ሠራዊት አዛዥ በሆነው በሲሣራ እጅ፥ በፍልስጥኤማውያን እጅና በሞአብ ንጉሥ እጅ ሸጣቸው፤ እነዚህ ሁሉ አባቶቻችሁን ተዋጓቸው። 10 እነርሱም ወደ እግዚአብሔር በመጮህ፥ "እግዚአብሔርን ትተን በኣልንና አስታሮትን በማገልገላችን ኃጢአት አድርገናል። አሁን ግን ከጠላቶቻችን እጅ አድነን፥ እኛም እናገለግልሃለን' አሉት። 11 ስለዚህ እግዚአብሔር ይሩበኣልን፥ ባርቅን፥ ዮፍታሔንና ሳሙኤልን ልኮ በሰላም እንድትኖሩ በዙሪያችሁ ባሉ ጠላቶቻችሁ ሁሉ ላይ ድልን ሰጣችሁ። 12 እናንተም የአሞን ሕዝብ ንጉሥ ናዖስ እንደመጣባችሁ ባያችሁ ጊዜ፥ አምላካችሁ እግዚአብሔር ንጉሣችሁ ሆኖ እያለ፥ 'አይሆንም፥ ይልቁን በላያችን ላይ ንጉሥ መንገሥ አለበት' አላችሁኝ። 13 አሁንም እናንተ የመረጣችሁት፥ እንዲሆንላችሁ የጠየቃችሁትና እግዚአብሔርም በእናንተ ላይ ንጉሥ እንዲሆን የመረጠው ንጉሥ ይኸውላችሁ። 14 እናንተም እግዚአብሔርን ብትፈሩት፥ ብታገለግሉት፥ ድምፁንም ብትታዘዙና በእግዚአብሔር ትዕዛዝ ላይ ባታምጹ ያን ጊዜ እናንተና በላያችሁ የሚገዛው ንጉሣችሁ የአምላካችሁ የእግዚአብሔር ተከታዮች ትሆናላችሁ። 15 የእግዚአብሔርን ድምፅ ባትታዘዙ፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ትዕዛዝ ላይ ብታምጹ፥ ያን ጊዜ በአባቶቻችሁ ላይ እንደነበረ የእግዚአብሔር እጅ በእናንተ ላይ ይሆናል። 16 አሁንም፥ ራሳችሁን አቅርቡና እግዚአብሔር በዓይናችሁ ፊት የሚያደርገውን ይህንን ታላቅ ነገር ተመልከቱ። 17 ዛሬ የስንዴ መከር ነው አይደል? ነጎድጓድና ዝናብን እንዲልክ እግዚአብሔርን እጠራለሁ። ከዚያም ለራሳችሁ ንጉሥ በመጠየቃችሁ በእግዚአብሔር ፊት ያደረጋችሁት ክፋት ታላቅ እንደሆነ ታውቃላችሁ፥ ታያላችሁም“። 18 ስለዚህ ሳሙኤል እግዚአብሔርን ጠራ፤ በዚያው ቀን እግዚአብሔር ነጎድጓድንና ዝናብን ላከ። ሕዝቡም ሁሉ እግዚአብሔርንና ሳሙኤልን በጣም ፈሩ። 19 ከዚያም ሕዝቡ ሁሉ ሳሙኤልን፥ "እንዳንሞት፥ ስለ አገልጋዮችህ ወደ አምላክህ ወደ እግዚአብሔር ጸልይ። ለራሳችን ንጉሥ በመጠየቃችን በኃጢአታችን ሁሉ ላይ ይህንን ክፋት ጨምረናልና” አሉት። 20 ሳሙኤል እንዲህ ሲል መለሰላቸው፥ “አትፍሩ። ይህንን ሁሉ ክፋት አድርጋችኋል፥ ነገር ግን እግዚአብሔርን በሙሉ ልባችሁ አገልግሉት እንጂ ከእግዚአብሔር ፊታችሁን አትመልሱ። 21 የማይጠቅሙ ናቸውና ሊረዷችሁ ወይም ሊረቧችሁ የማይችሉትን ከንቱ ነገሮች አትከተሉ። 22 እግዚአብሔር የራሱ ሕዝብ ሊያደርጋችሁ ስለ ወደደ፥ ስለ ታላቅ ስሙ ሲል ሕዝቡን አይጥላቸውም። 23 ስለ እናንተ መጸለይን በመተው በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአትን ማድረግ ከእኔ ይራቅ። ይልቁንም፥ መልካሙንና ትክክለኛውን መንገድ አስተምራችኋለሁ። 24 ብቻ እግዚአብሔርን ፍሩት፥ በሙሉ ልባችሁም በእውነት አገልግሉት። ያደረገላችሁን ታላላቅ ነገሮች አስቡ። 25 ክፉ በማድረግ ብትጸኑ ግን እናንተና ንጉሣችሁ ትጠፋላችሁ”።



1 Samuel 12:1

ንጉሡ በፊታችሁ ይሄዳል … እኔም በፊታችሁ ሄድሁ

እነዚህ መግለጫዎች ሳሙኤልና ሳኦል የኖሩትን የሕይወት ዓይነት ሕዝቡ በተጨባጭ ማየት ችሏል ማለት ነው፡፡ አት፡- "የንጉሡ ሕይወት ታይቷል … የእኔ ሕይወት ታይቷል' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 12:3

በዚህ አለሁ፣በእግዚአብሔርና እርሱ በቀባው ፊት መስክሩብኝ

በዚህ ንግግሩ ሳሙኤል አንዳች ተገቢ ያልሆነ ነገር በማንም ላይ አድርጎ ከሆነ ሕዝቡ እንዲናገር እየሞገተ ነው፡፡ አት፡- "አሁን በፊታችሁ ቆሜያለሁ፡፡ ምንም ዓይነት ተገቢ ያልሆነ ነገር አድርጌ ከሆነ በእግዚአብሔርና በቀባው በንጉሡ ፊት እንድትናገሩ እጠይቃችኋለሁ፡፡' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

የማንን በሬ ወሰድሁ? የማንንስ አህያ ወሰድሁ?

እንሰሳቶቻቸውን ያልሰረቀባቸውን ሰዎች ለማሳሳብ ሳሙኤል አሳብ ገላጭ ጥያቄ ይጠቀማል፡፡ አት፡- "እኔ ውድ የሆነ እንስሳ ፈጽሞ ከማንም አልሰረቅሁም' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ማንንስ ሸነገልሁ

ሁልጊዜ ታማኝ እንደ ነበር ለመናገር ሳሙኤል ሌላ አሳብ ገላጭ ጥያቄ ይጠቀማል፡፡ አት፡- "እኔ ማንንም አልታለልኩም ወይም ከማንም ጉቦ አልተቀበልሁም፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

መስክሩብኝ እኔም እመለሳለሁ

"ከእነዚህ ክፉ ነገሮች ማናቸውንም አድርጌ ከሆንሁ አሁን ተናገሩ፣ የወሰድኩትንም እመለሳለሁ፡፡ ማናኛውንም ስሕተት አስተካክላለሁ፡፡'

1 Samuel 12:4

ከማንም እጅ … በእጄ

እነዚህ ሃረጎች ግለሰቡ ምን ሃብት እንዳፈራ ወይም ከሌሎች ወሮታን ለማግኘት ምን እንዳደረገ የሚገልጽ ነው፡፡ አት፡- ይህ ምንም እንዳልሰረቀ፣ ወይም ጉቦ እንዳልሰጠና እንዳልተቀበለ የተናገረበት ጨዋ መንገድ ነው፡፡

1 Samuel 12:6

የእግዚአብሔር የጽድቅ ሥራ ሁሉ

በመልካምነትና በዓላማ ለተሞላው፣ እግዚአብሔር ለእስራኤል ላደረገው ታሪክ ትኩረት እንዲሰጡ ሳሙኤል አየተጣራ ነው፡፡

1 Samuel 12:8

ለሲሣራ … ለፍልስጥኤማውያን … ለሞአብ ንጉሥ እጅ

"ለሲሣራ … ለፍልስጥኤማውያን … ለሞአብ ንጉሥ ኃይል'

ያዕቆብ … ሙሴ … አሮን … ሲሣራ

እነዚህ የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

አዞር

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

ሸጣቸው

ይህ ባሮቻቸው እንዲሆኑ እግዚአብሔር ለጠላቶቻቸው አሳልፎ መስጠቱን የሚገልጽ ነው፡፡

1 Samuel 12:10

ወደ እግዚአብሔር ጮኹ

(እነርሱ) የእስራኤልን ሕዝብ የሚያመለክት ነው

ይሩ ባአል

ይህ አንዳንዴ ይሩባአል በሚል ይተረጎማል፡፡ ይህ ሐሰተኛ አማልከትን ለመዋጋት የጻድቅ የክብርና የጥንካሬ ስም ነው፡፡

እግዚአብሔር ላከ … ድልም ሰጣችሁ

ሳሙኤል ከሕዝቡ የኃጢአት ኑዛዜና የእርዳታ ጥሪ በኋላ እግዚአብሔር ምን እንዳደረገላቸው ታሪኩን ይናገራል፡፡ (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ይሩ ባአል፣ ባርቅ፣ ዮፍታሔና ሳሙኤል

እነዚህ እግዚአብሔር ያስነሳቸወ ጥቂት የመሳፍንት ስሞች ናቸው፡፡ ሳሙኤል ራሱን በዚህ ዝርዝር ውስጥ አካቷል፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

በአሊምንና አስታሮትን አገለገሉ

በዚህ ስፍራ ማገልገል ሐሰተኛ አማልክትን የማምለክን ተግባር ያመለክታል፡፡ አት፡- ሐሰተኛ አማልክትና ሴት አማልክትን አመለኩ (ምትክ ቃል ተመልከት)

የጠላቶቻችን እጅ

ይህ አረፍተ ነገር ኃይልን ለማመልከት "እጅ' የሚለውን ቃል ይጠቀማል፡፡ አት፡- "የጠላቶቻችን ኃይል ወይም የበላይነት' (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 12:12

እንዲህ አይሁን! ነገር ግን ንጉሥ ይንገሥልን

ይህ አረፍተ ነገር እግዚአብሔር ትናንትና ስላዳናቸው በእግዚአብሔር ስለመታመን በነገራቸው ጊዜ የእስራኤል ሕዝብ ሳሙኤልን በመቃወም ስላሰዩት ብርቱ ምላሽ ይናገራል፡፡

የመረጣችሁትንና የጠየቃችሁትን

እነዚህ ሁለት ቃላት ሕዝቡ የፈለገው ንጉሥ ይህ ነው የሚል ተመሣሣይ ትርጉምና አጽንዖት አላቸው፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

1 Samuel 12:14

ብትፈሩ … ብታገለግሉ … ብትታዘዙ … ባታምጹ

ይህ ምን ያህል አስፈላጊ እነደሆነ አጽንዖት ለመስጠት እነዚህ ተመሣሣይ ቃላት ጥቅም ላይ ውለዋል፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

በአባቶቻችሁ ላይ እንደሆነ፣ የእግዚአብሔር እጅ በእናንተ ላይ ትሆናለች

ይህ እጁ በእነርሱ ላይ እነደሆነች ሁሉ እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደሚቀጣ ይናገራል፡፡ በዚህ ስፍራ "እጅ' የሚለው ቃል የእግዚአብሔርን ኃይልና የበላይነት ይወክላል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር አባቶቻችሁን እንደቀጣ ይቀጣችኋል' (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 12:16

በዓይኖቻችሁ ፊት

በዚህ ስፍራ "ዓይኖች' የሚለው ቃል የእስራኤልን ሕዝብ ይወክላል፡፡ አት፡- "የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ ሊያይ በሚችልበት ግልጽ ስፍራ' (ተለዋጭ ቃል ተመልከት)

የስንዴ መከር ዛሬ አይደለምን?

ሳሙኤል የመከር ጊዜ እንደሆነ ያውቃል፡፡ በአብዛኛው በዚህ ጊዜ ዝናብ እንደማይዘንብ ስለዚህ የእግዚአብሔር ፍርድ በመሆኑ ዝናቡ መከራቸውን እንደሚያጠፋ ሕዝቡ እንዲያውቅ አጽንዖት ለመስጠት አሳብ ገላጭ ጥያቄ ይጠቀማል፡፡ አት፡- "የመከር ጊዜ ነው በአብዛኛውም በዚህ ጊዜ አይዘንብም' (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ነጎድጓድና ዝናብ ይልካል

ሳሙኤል በመከር ጊዜ እህሉን የሚያጠፋ ከባድ ዝናብ በመላክ ንጉስ ስለመጠየቃቸው እግዚአብሔር እሥራኤልን እንዲቀጣ ይጠይቃል፡፡

1 Samuel 12:19

እንዳንሞት

የኃጢአት የመጨረሻ ቅጣት ሞት ነው፡፡ እግዚአብሔር ይጨቁኗቸው የነበሩትን ሕዝቦቸ እንዳጠፋ የእስራኤል ሕዝብ አይቷል፡፡ እንደሌሎቹ ሕዝቦች "ለጥፋት እንዳይሰጡ' ተጨንቀው ነበር፡፡

አትፍሩ

ሕዝቡ ክፉ አደረጉ እንዳያጠፋቸውም እግዚአብሔርን ፈሩ፡፡ አት፡- "ከዚህ ኃጢአት የተነሣ እግዚአብሔር ይቆጣል ያጠፋናልም ብላችሁ አትፍሩ' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ከንቱ ነገርን ለመከተል ፈቀቅ አትበሉ

"ሐሰተኛ አማልክትን ማምለክ አትከታተሉ'

1 Samuel 12:22

ስለ ታላቅ ስሙ

በዚህ ስፍራ ስም የእግዚአብሔርን ክብር ያመላክታል፡፡ አት፡- "ስለዚህ ሕዝቡ እግዚአብሔርን በማክበርና በመፍራት ይኖራል፡፡' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ስለ እናንተ መጸለይን በመተው እግዚአብሔርን እበድል ዘንድ ይህ ከእኔ ይራቅ

ሳሙኤል በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔር ከላከው ዝናብና ነጎድጓድ የተነሣ ሕዝቡ በፍርሃት ተሞላ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ሳሙኤል ጸሎቱን እነርሱን ለመጉዳት ሊጠቀምበት እንደሚችል ሳያምኑ አልቀሩም፡፡ (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)


Chapter 13

1 ሳኦል መንገሥ በጀመረ ጊዜ ዕድሜው ሠላሳ ዓመት ነበር፤ በእስራኤል ላይ አርባ ዓመት በነገሠ ጊዜ፥ 2 ከእስራኤል ሦስት ሺህ ሰዎች መረጠ። አንዱ ሺህ ከዮናታን ጋር በብንያም ጊብዓ ሲሆኑ ሁለቱ ሺህ በኮረብታማው አገር በቤቴልና በማክማስ ከእርሱ ጋር ነበሩ። የቀሩትን ወታደሮች ወደየቤታቸው፥ እያንዳንዱንም ወደ ድንኳኑ አሰናበታቸው። 3 ዮናታን በጊብዓ የነበረውን የፍልስጥኤማውያን ጦር ድል አደረገ፥ ፍልስጥኤማውያንም ይህንን ሰሙ። ከዚያም ሳኦል፥ “ዕብራውያን ይስሙ” በማለት በምድሪቱ ሁሉ ላይ መለከት አስነፋ። 4 ሳኦል የፍልስጥኤማውያንን ጦር እንዳሸነፈ፥ ደግሞም እስራኤላውያን በፍልስጥኤማውያን እንደ ግም መቆጠራቸውን እስራኤላውያን በሙሉ ሰሙ። ከዚያም ወታደሮቹ በጌልገላ ሳኦልን ለመከተል በአንድ ላይ ተሰበሰቡ። 5 ፍልስጥኤማውያንም ከእስራኤል ጋር ለመዋጋት በአንድ ላይ ተሰበሰቡ፤ ሦስት ሺህ ሠረገሎች፥ ስድስት ሺህ ሠረገላ ነጂዎችና የሠራዊቱም ቁጥር በባህር ዳርቻ እንዳለ አሸዋ ነበሩ። እነርሱም መጥተው ከቤትአዌን በስተምሥራቅ ማክማስ ላይ ሰፈሩ። 6 የእስራኤል ሰዎች ችግር ውስጥ መግባታቸውንና ሕዝቡም መጨነቁን ባዩ ጊዜ፥ ሕዝቡ በዋሻዎች፥ በየቁጥቋጦ ሥር፥ በዐለቶች፥ በገደሎችና በጉድጓዶች ውስጥ ተደበቁ። 7 አንዳንድ ዕብራውያንም የዮርዳኖስን ወንዝ በመሻገር ወደ ጋድና ገለዓድ ምድር ሄዱ። ሳኦል ግን ገና በጌልገላ ነበር፥ የተከተለው ሕዝብ በሙሉ በፍርሃት ይንቀጠቀጥ ነበር። 8 እርሱም ሳሙኤል በሰጠው ቀጠሮ መሠረት ሰባት ቀን ቆየ። ነገር ግን ሳሙኤል ወደ ጌልገላ አልመጣም ነበር፥ ሕዝቡም ከሳኦል ተለይቶ መበታተን ጀምሮ ነበር። 9 ሳኦልም፥ "የሚቃጠለውን መባና የሰላሙን መባዎች አምጡልኝ" አለ። ከዚያም የሚቃጠለውን መባ አቀረበ። 10 የሚቃጠለውን መባ ማቅረቡን እንደ ጨረሰ ሳሙኤል ወደዚያ ደረሰ። ሳኦልም ሊገናኘውና ሰላምታ ሊሰጠው ሄደ። 11 ከዚያም ሳሙኤል፥ "ያደረግከው ምንድነው?" አለው። ሳኦልም፥ "ሕዝቡ ትተውኝ እየሄዱ እንዳሉ፥ አንተም በቀጠሮው ሰዓት አለመምጣትህን፥ ፍልስጥኤማውያንም በማክማስ መሰብሰባቸውን ባየሁ ጊዜ፥ 12 'አሁን ፍልስጥኤማውያን ወደ ጌልገላ በእኔ ላይ ሊወርዱብኝ ነው፥ እኔም የእግዚአብሔርን ሞገስ አልለመንኩም' ብዬ አሰብኩኝ። ስለዚህ የሚቃጠለውን መሥዋዕት ለማቅረብ ግድ ሆነብኝ“ ብሎ መለሰለት። 13 ሳሙኤልም ሳኦልን፥”ያደረግከው ስንፍና ነው። አምላክህ እግዚአብሔር የሰጠህን ትዕዛዝ አልጠበቅክም። በዚህ ቀን እግዚአብሔር መንግሥትህን በእስራኤል ላይ ለዘላለም ሊያጸናልህ ነበር። 14 አሁን ግን አገዛዝህ አይቀጥልም። እግዚአብሔር ያዘዘህን አልታዘዝክምና እርሱ እንደ ልቡ የሚሆንለትን ሰው ፈልጓል፥ እግዚአብሔርም በሕዝቡ ላይ መስፍን እንዲሆን መርጦታል" አለው። 15 ከዚያም ሳሙኤል ከጌልገላ ተነሥቶ ወደ ብንያም ጊብዓ ወጣ። ሳኦል ከእርሱ ጋር የነበሩትን ሰዎች ቆጠራቸው፥ ስድስት መቶ የሚያክሉ ነበሩ። 16 ሳኦል፥ ልጁ ዮናታንና ከእነርሱ ጋር የነበሩት ሰዎች በብንያም ጊብዓ ቆዩ። ፍልስጥኤማውያን ግን በማክማስ ሰፍረው ነበር። 17 ከፍልስጥኤም ጦር ሰፈር ወራሪዎች በሦስት ቡድን ተከፍለው መጡ። አንደኛው ቡድን ወደ ሦጋል ምድር ወደ ዖፍራ ታጠፈ። 18 ሌላኛው ቡድን በቤትሖሮን አቅጣጫ ታጠፈ፥ ሌላኛውም ቡድን በምድረ በዳው አቅጣጫ ወደ ስቦይም ሸለቆ ቁልቁል ወደሚያሳየው ወሰን ዞረ። 19 ፍልስጥኤማውያን፥ “ዕብራውያን ለራሳቸው ሰይፍ ወይም ጦር እንዳይሠሩ" ብለው ስለነበረ፥ በመላው እስራኤል ብረት ሠሪ አልተገኘም። 20 ነገር ግን የእስራኤል ወንዶች ሁሉ፥ እያንዳንዱ የማረሻውን ጫፍ፥ ዶማውን፥ ጠገራውንና ማጭዱን ለማሳል ወደ ፍልስጥኤማውያን ይወርድ ነበር። 21 የክፍያው ዋጋ ለማረሻው ጫፍና ለዶማው የሰቅል ሁለት ሦስተኛ፥ ጠገራ ለማሳልና መውጊያውን ለማቃናት የሰቅል አንድ ሦስተኛ ነበር። 22 ስለዚህ በጦርነቱ ቀን ሰይፍና ጦር በሳኦልና በዮናታን እጅ ብቻ እንጂ ከእነርሱ ጋር ከነበሩት ወታደሮች በአንዱም እጅ ሰይፍ ወይም ጦር አልነበረም። 23 የፍልስጥኤማውያን ሠራዊት ወደ ማክማስ መተላለፊያ ወጣ።



1 Samuel 13:1

አጠቃላይ መረጃ

ሳሙኤል በጌልጌላ የሳኦልን መንግሥት አደሰለት ሳሙኤልም ጌታን እንዲከተሉ ሕዝቡን አሳሰበ፡፡

ሳኦል ሠላሣ ሁለት ዓመቱ ነበር … በእስራኤልም ላይ

በጥንት ቅጂዎች የዚህ ጥቅስ ጽሑፍ የተጎዳ ይመስላል፣ ስለዚህ የዘመናችን እትሞች የተለያዩ ትርጉሞችን ይዘዋል፡፡ ሁሉም ሊሆን የሚችለውን የተሻለውን የመጀመሪያውን ጽሑፍ ትርጉም ለማቅረብ ጥረት አድርገዋል፡፡

ሦሥት ሺህ ሰዎች መረጠ

"3,000 ሰዎች መረጠ' (ቁጥሮች ተመልከት)

ሁለት ሺህ ሰዎች ከእርሱ ጋር ነበሩ

"2,000 ሰዎች ከእርሱ ጋር ነበር' (ቁጥሮች ተመልከት)

ማክማስ

የከተማ ስም ነው (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

የብንያም ጊብዓ

ጊብዓ ከተማ ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 10፡26 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

የቀሩትን ወታደሮች ወደ ቤት ሰደዳቸው

"የቀሩትን ወታደሮች ቤት ሰደዳቸው'

1 Samuel 13:3

የፍልስጥኤማውያን ጭፍራ

"የፍልስጥኤማውያን የጦር ሰፈር'

ናሲብ

ይህ የፍልስጥኤም ጭፍራ የሰፈረበት የከተማ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ሳኦል እንዳሸነፈ እስራኤላውያን ሁሉ ሰሙ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች፡- 1) ዮናታን ለፈጸመው ጥቃት ሳኦል ኃላፊነቱን እየወሰደ ነበር ወይም 2) ዮናታን በፈጸመው ጥቃት የተገኘውን ድል ሳኦል እየወሰደ ነበር

እስራኤል ለፍልስጥኤም እንደ ብስባሽ ሽታ ሆነች

ፍልስጥኤማውያን ለእስራኤል ያላቸው ጥላቻ እስራኤላውያን ፍልስጥኤማውያንን የሚረብሽ መጥፎ ሽታ እንደሆኑ ተደርጎ ተገለጾአል፡፡ አት፡- "ፍልስጥኤማውያን እስራኤላውያንን ጠሉአቸው' (ዘይቤአዊ አነጋገር ተመልከት)

ወታደሮቹ ሳኦልን ለመከተል ወደ ጌልጌላ ተሰበሰቡ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- ሳኦል ወታደሮቹ እንዲከተሉት በጌልጌላ እንዲሰበሰቡ ጠራቸው (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

1 Samuel 13:5

ሦሥት ሺህ … ስድስት ሺህ

"3000 … 6000' (ቁጥሮች ተመልከት)

ወታደሮቹ በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ ብዙ ነበሩ

ለመቁጠር እስከሚያስቸግር ድረስ የወታደሮቹ ስብስብ ታላቅ ነበር የሚል ግነት ነው፡፡ (ግነትና አጠቃላይነት ተመልከት)

ማክማስ

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ቤትአዌን

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 13:6

አጠቃላይ መረጃ

ፍልስጥኤማውያን እስራኤልን ለመዋጋት በአንድነት ተሰበሰቡ፡፡

ሕዝቡ

ይህ ሐረግ የእስራኤልን ሕዝብ ያመለክታል፡፡

ሕዝቡ ታውኮ ነበር

"ሕዝቡ በጣም ተጨንቆ ነበር'

ተንቀጥቅጠው ተከተሉት

ሕዝቡ በጣም ፈርተው ነበር

1 Samuel 13:8

ሳሙኤል በቀጠረው ቀን

"እንደሚመጣ ሳሙኤል በነገራቸው ጊዜ መሠረት'

ሕዝቡ ከሳኦል ተለይተው ተበታተኑ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "ሕዝቡ ሳኦልን ትቶ መሄድ ጀመረ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ)

ከዚያም የሚቃጠል መሥዋዕት አቀረበ

የሚቃጠል መሥዋዕትን ለእግዚአብሔር ማቅረብ የተፈቀደው ለአሮን ወገን ብቻ ነበር

1 Samuel 13:11

ያደረግኸው ምንድር ነው?

በእውነቱ ሳሙኤል እየጠየቀ ሳይሆን ሳኦልን እየገሰጸው ነበር፡፡ ትክክል ባይሆኑም እንኳን ሳኦል ለድርጊቶቹ ሊከላከል ፈለገ፡፡ (አሳብ ገላጭ ጥያቄዎች ተመልከት)

ማክማስ

ማክማስ የቦታ ስም ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 13፡2 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

1 Samuel 13:13

የእግዚአብሔርን ትእዛዝ አልጠበቅህም

ሳሙኤል እስኪመጣና ለእግዚብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት እስኪሰዋ ድረስ ሳኦል መጠበቅ ነበረበት፡፡ እርሱ ራሱ መሠዋት አልነበረበትም፡፡

መንግሥትህን አጽንቶልህ ነበር

"መንግሥትህን አቁሞልህ ነበር' ወይም "መንግሥትህን አውቆልህ ነበር' ወይም "መንግሥትህን መርጦ ነበር'

መንግሥትህ አይቀጥልም

ይህ በአዎንታዊ መንገድ የቀረበ ምፀት ነው፡፡ አት፡- "መንግሥትህ በቅርቡ ያከትማል' (ምፀት ተመልከት)

እንደ ልቡ የሆነ ሰው

በዚህ ስፍራ ልብ የእግዚአብሔርን ፍላጎትና ፈቃድ ይወክላል፡፡ "እንደ ልቡ የሆነ ሰው' የሚለው ሐረግ እግዚአብሔር የሚፈልገውን የሚያደርግ ሰው የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "ይፈልገው የነበረ ዓይነት ሰው' ወይም "የሚታዘዘው ሰው' (ምትክ ቃልና ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 13:15

ሳሙኤል ተነሣና ሄደ

"ሳሙኤል ትቶ ሄደ' ለሚለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ከጌልጌላ ተነስቶ ሄደ

ጌልጌላ ከተማ ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 7፡15 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

የብንያም ጊብዓ

ጊብዓ ከተማ ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 10፡26 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

ስድስት መቶ ሰዎች

"600 ሰዎች' (ቁጥሮች ተመልከት)

የብንያም ጊብዓ

ጊብዓ ከተማ ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 13፡03 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

ፍልስጥኤማውያን በማክማስ ሰፈሩ

ማክማስ የቦታ ስም ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 13፡02 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

1 Samuel 13:17

አደጋ ጣዮች መጡ

አደጋ ጣዮች በአብዛኛው ለምግባቸውና ሌሎች ቁሳ ቁሶች በጠላት መንደር ላይ ጥቃት የሚያደርሱ የጦር ሰዎች ናቸው፡፡

ዖፍራ … ሦጋል ምድር … ቤትሐሮን … ስቦይም ሸለቆ

እነዚህ የቦታ ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 13:22

አጠቃላይ መረጃ

ታሪኩ ይቀጥላል፡፡

ሰይፍና ጦር አልነበረም

ይህ ለምን የሳኦል ሠራዊት እንደፈሩ በከፊል ያሳያል፡፡


Chapter 14

1 አንድ ቀን የሳኦል ልጅ ዮናታን ወጣቱን ጋሻ ጃግሬውን፥”ና፥ በፍልስጥኤማውያን ሠራዊት ላይ በሌላ አቅጣጫ እንሂድባቸው“ አለው። ለአባቱ ግን አልነገረውም። 2 ሳኦል መጌዶን በሚባል በጊብዓ ዳርቻ በሮማኑ ዛፍ ሥር ሰፍሮ ነበር። 3 እርሱም በሴሎ የእግዚአብሔር ካህን የነበረው የዔሊ ልጅ፥ የፊንሐስ ልጅ፥ የኢካቦድ ወንድም የአኪጦብ ልጅ የሆነው፥ ኤፉድ ይለብስ የነበረውን አኪያን ጨምሮ ስድስት መቶ ያህል ሰዎች ከእርሱ ጋር ነበሩ። ዮናታን መሄዱን ሕዝቡ አላወቀም ነበር። 4 ዮናታን ወደ ፍልስጥኤማውያኑ ጦር ሰፈር አቋርጦ ለመሄድ ባሰበባቸው በመተላለፊያዎቹ መካከል በግራና በቀኙ በኩል ሾጣጣ ድንጋዮች ነበሩ። የአንደኛው ሾጣጣ ድንጋይ ስም ቦጼጽ ሲሆን የሁለተኛው ስም ሴኔ ነበር። 5 አንደኛው ቀጥ ያለው ድንጋይ የቆመው በስተሰሜን በሚክማስ ፊት ለፊት ሲሆን ሌላኛው በጊብዓ ፊት ለፊት በስተደቡብ ነበር። 6 ዮናታንም ወጣት ጋሻ ጃግሬውን፥ "ና፥ ወደእነዚህ ወዳልተገረዙት ጦር ሰፈር እንሻገር። እግዚአብሔር በብዙ ወይም በጥቂት ሰዎች ከማዳን ሊከለክለው የሚችል ነገር የለምና፥ ምናልባት እግዚአብሔር ይሠራልን ይሆናል" አለው። 7 ጋሻ ጃግሬውም፥ "በልብህ ያለውን ሁሉ አድርግ። ወደፊት ቀጥል፥ ተመልከት፥ የምታዝዘኝን ሁሉ ለመፈጸም ከአንተ ጋር ነኝ" ብሎ መለሰለት። 8 ከዚያም ዮናታን እንዲህ አለው፥ "ወደ እነርሱ ተሻግረን እንታያቸዋለን። 9 እነርሱም፥ 'ወደ እናንተ እስክንመጣ እዚያው ቆዩ' ካሉን በስፍራችን እንቆያለን፥ ወደ እነርሱም አንሻገርም። 10 ነገር ግን፥ 'ወደ እኛ ውጡ' ብለው ቢመልሱልን እግዚአብሔር በእጃችን አሳልፎ ሰጥቶናልና ወደ እነርሱ እንሻገራለን።” 11 ስለዚህ ሁለቱም ራሳቸውን ለፍልስጥኤማውያን ጦር ገለጡ። ፍልስጥኤማውያኑም፥ “ተመልከቱ፥ ዕብራውያኑ ከተደበቁባቸው ጉድጓዶች ወጥተው እየመጡ ነው" ተባባሉ። 12 ከዚያም የጦር ሰፈሩ ሰዎች ወደ ዮናታንና ጋሻ ጃግሬው በመጣራት፥”ወደ እኛ ውጡ፥ አንድ ነገርም እናሳያችኋለን" አሏቸው። ዮናታን ጋሻ ጃግሬውን፥ “እግዚአብሔር በእስራኤል እጅ አሳልፎ ሰጥቷቸዋልና ተከተለኝ" አለው። 13 ዮናታን በእጁና በእግሩ ተንጠላጥሎ ወጣ፥ ጋሻ ጃግሬውም ከኋላው ተከተለው። ፍልስጥኤማውያኑ በዮናታን ተገደሉ፥ ጋሻ ጃግሬውም ከኋላው ተከትሎ ጥቂቶቹን ገደለ። 14 ዮናታንና ጋሻ ጃግሬው በፈጸሙት በዚያ የመጀመሪያ ጥቃት አንድ ጥማድ በሬ ሊያርሰው በሚችለው የመሬት ስፋት ላይ ሃያ ያህል ሰዎችን ገደሉ። 15 በጦር ሰፈሩ፥ በእርሻውና በሕዝቡ መካከል ሽብር ሆነ። የጦር ሰፈሩና ወራሪዎቹም እንኳን ተሸበሩ። ምድሪቱ ተንቀጠቀጠች፥ ታላቅ ሽብርም ሆነ። 16 በብንያም ጊብዓ የነበሩ የሳኦል ጠባቂዎች፥ የፍልስጥኤም ወታደሮች ሲበተኑና ወዲያና ወዲህ ሲራወጡ ተመለከቱ። 17 ከዚያም ሳኦል ከእርሱ ጋር ለነበሩት ሰዎች፥”ቁጠሩና ከእኛ የጎደለ ማን እንደሆነ ዕወቁ“ አላቸው። በቆጠሩ ጊዜም ዮናታንና ጋሻ ጃግሬው ታጡ። 18 ሳኦልም አኪያን፥ "የእግዚአብሔርን ኤፉድ ወደዚህ አምጣው" አለው። በዚያ ቀን አኪያ ኤፉድ ለብሶ ከእስራኤል ወታደሮች ጋር ነበር። 19 ሳኦል ከካህኑ ጋር በመነጋገር ላይ እያለ በፍልስጥኤማውያን የጦር ሰፈር የነበረው ሁከት መጨመሩን ቀጠለ። ሳኦልም ካህኑን፥ "እጅህን መልስ" አለው። 20 ሳኦልና ከእርሱ ጋር የነበሩት ሰዎች ሁሉ በሩጫ ወደ ጦርነቱ ሄዱ። የእያንዳንዱ ፍልስጥኤማዊ ሰይፍ በራሱ ዜጋ ላይ ነበር፥ ታላቅ ግራ መጋባት ውስጥ ነበሩ። 21 ቀድሞ ከፍልስጥኤማውያን ጋር የነበሩና አብረዋቸው ወደ ጦር ሰፈሩ የገቡት ዕብራውያን እነርሱም እንኳን አሁን ከሳኦልና ከዮናታን ጋር ከነበሩት እስራኤላውያን ጋር ተባበሩ። 22 በኤፍሬም አቅራቢያ በኮረብታዎቹ ውስጥ የተደበቁ የእስራኤል ሰዎች ሁሉ ፍልስጥኤማውያን መሸሻቸውን በሰሙ ጊዜ እነርሱም እንኳን ለውጊያ በኋላቸው አሳደዷቸው። 23 ስለዚህ እግዚአብሔር በዚያን ቀን እስራኤልን አዳነ፥ ውጊያውም ቤትአዌንን አልፎ ሄደ። 24 ሳኦል፥”ጠላቶቼን እስከምበቀልበት እስከ ምሽት ድረስ የትኛውንም ዓይነት መብል የሚበላ ቢኖር የተረገመ ይሁን“ ብሎ ሕዝቡን አምሎ ስለነበረ በዚያን ቀን የእስራኤል ሰዎች ተጨነቁ። ስለዚህ ከሠራዊቱ አንዱም ምግብ አልቀመሰም። 25 ከዚያም ሕዝቡ ሁሉ ወደ ጫካ ውስጥ ገባ፥ ማርም በምድሩ ላይ ነበር። 26 ሕዝቡ ወደ ጫካ በገባ ጊዜ ማሩ ይፈስስ ነበር፥ ነገር ግን ሕዝቡ መሓላውን ስለፈራ በእጁ ጠቅሶ ወደ አፉ ያደረገ አንድም አልነበረም። 27 ዮናታን ግን አባቱ ሕዝቡን በመሓላ ማሰሩን አልሰማም ነበር። በእጁ ላይ የነበረውን በትር ጫፉን በማሩ እንጀራ ውስጥ አጠቀሰው። እጁን አንሥቶ ወደ አፉ አደረገው፥ ዐይኖቹም በሩለት። 28 ከዚያም ከሰዎቹ አንዱ፥”ሕዝቡ በረሃብ ቢደክምም እንኳን አባትህ፥ 'በዚህ ቀን ምግብ የሚበላ የተረገመ ይሁን' ብሎ ሕዝቡን ከመሓላ ጋር አጥብቆ አዝዞአል" ብሎ መለሰለት። 29 ከዚያም ዮናታን፥ "አባቴ በምድሪቱ ላይ ችግር ፈጥሯል። ከዚህ ማር ጥቂት በመቅመሴ ዐይኖቼ እንዴት እንደበሩ ተመልከቱ። 30 ሕዝቡ ከጠላቶቻቸው ከበዘበዙት ላይ ዛሬ በነጻነት በልተው ቢሆን ኖሮ ምንኛ በተሻለ ነበር? ምክንያቱም አሁን በፍልስጥኤማውያን መካከል የተገደሉት ያን ያህል ብዙ አይደሉም“ አለ። 31 እነርሱም በዚያን ቀን ፍልስጥኤማውያንን ከሚክማስ ጀምሮ እስከ ኤሎን ድረስ መቱአቸው። ሕዝቡም እጅግ ደከሙ። 32 ሕዝቡም ተስገብግበው ወደ ብዝበዛው ተጣደፉ፥ በጎችን፥ በሬዎችንና ጥጆችንም በመሬት ላይ አረዱ። ሕዝቡም ከነደሙ በሉ። 33 ከዚያም ለሳኦል፥ "ተመልከት፥ ሕዝቡ ከነደሙ በመብላታቸው በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት በመሥራት ላይ ናቸው" አሉት። ሳኦልም፥ "ተላልፋችኋል፥ አሁንም ትልቅ ድንጋይ አንከባልላችሁ አምጡልኝ“ አለ። 34 በመቀጠልም፥ "ወደ ሕዝቡ ሂዱና፥ 'እያንዳንዱ ሰው በሬውንና በጉን እዚህ አምጥቶ በማረድ ይብላ። ከነደሙ በመብላት በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአትን አታድርጉ' ብላችሁ ንገሯቸው" አለ። ስለዚህ በዚያ ምሽት እያንዳንዱ በሬውን እያመጣ በዚያ ዐረደው። 35 ሳኦል ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሠራ፥ ይኸውም ለእግዚአብሔር የሠራው የመጀመሪያው መሠዊያ ነበር። 36 ከዚያም ሳኦል፥ "ሌሊቱን ፍልስጥኤማውያንን እናሳድ፥ እስኪነጋም ድረስ ሀብታቸውን እንበዝብዝ፤ ከእነርሱም አንድ በሕይወት አናስቀር“ አለ። እነርሱም፥”መልካም መስሎ የታየህን ሁሉ አድርግ“ ብለው መለሱለት። ካህኑ ግን፥”እዚሁ እግዚአብሔርን እንጠይቅ“ አለ። 37 ሳኦልም እግዚአብሔርን እንዲህ ሲል ጠየቀ፥”ፍልስጥኤማውያንን ላሳድዳቸው? በእስራኤል እጅ አሳልፈህ ትሰጣቸዋለህ? “። ነገር ግን በዚያን ቀን እግዚአብሔር አልመለሰለትም። 38 ከዚያም ሳኦል፥”የሕዝቡ አለቆች የሆናችሁ ሁሉ ወደዚህ ቅረቡ፤ ዛሬ ይህ ኃጢአት እንዴት እንደመጣብን መርምሩና ዕወቁ። 39 እስራኤልን ያዳነ ሕያው እግዚአብሔርን! ልጄ ዮናታን ቢሆን እንኳን በእርግጥ እርሱ ይሞታል" አለ። ነገር ግን ከሕዝቡ ሁሉ አንዱም እንኳን አልመለሰለትም። 40 እርሱም እስራኤልን በሙሉ፥ “እናንተ በአንድ በኩል ቁሙ፥ እኔና ልጄ ዮናታን በሌላው በኩል እንቆማለን” አላቸው። ሕዝቡም ሳኦልን፥ “መልካም መስሎ የታየህን አድርግ” አሉት። 41 ስለዚህ ሳኦል የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔርን፥ “በቱሚም አሳየኝ” አለው። ዮናታንና ሳኦል በዕጣ ተያዙ፥ ሕዝቡ ግን የተመረጠ ሆነና አመለጠ። 42 ከዚያም ሳኦል፥ “በእኔና በልጄ በዮናታን መክከል ዕጣ ጣሉ” አለ። ዮናታንም በዕጣ ተያዘ። 43 ሳኦልም ዮናታንን፥ “ያደረግኸውን ንገረኝ” አለው። ዮናታንም፥ “በእጄ በነበረው በትር ጫፍ ጥቂት ማር ቀምሻለሁ። ይኸው ለመሞት ዝግጁ ነኝ” አለ። 44 ሳኦልም፥ “ዮናታን ሆይ፥ ባትሞት እግዚአብሔር በእኔ ላይ እንዲሁ ያድርግ፥ ይጨምርም” አለ። 45 ሕዝቡም ሳኦልን፥ “ለእስራኤል ይህንን ታላቅ ድል ያመጣ ዮናታን መሞት ይገባዋል? ይህ ከእርሱ ይራቅ! እርሱ ዛሬ ከእግዚአብሔር ጋር ሠርቷልና ሕያው እግዚአብሔርን! ከራስ ጸጉሩ አንድ በምድር ላይ አይወድቅም" አሉት። ስለዚህ ሕዝቡ ዮናታንን ከመሞት አዳነው። 46 ከዚያም ሳኦል ፍልስጥኤማውያንን ማሳደዱን አቆመ፥ ፍልስጥኤማውያንም ወደ ስፍራቸው ሄዱ። 47 ሳኦል እስራኤልን መግዛት በጀመረ ጊዜ፥ በየአቅጣጫው ከነበሩ ጠላቶቹ ሁሉ ጋር ተዋጋ። እርሱም ከሞዓብ፥ ከአሞን ሰዎች፥ ከኤዶም፥ ከሱባ ነገሥታትና ከፍልስጥኤማውያን ጋር ተዋጋ። በደረሰበት ሁሉ በቅጣት ያሰቃያቸው ነበር። 48 ከአማሌቃውያን ጋር በጀግንነት ተዋግቶ ድል አደረጋቸው። እስራኤላውያንንም ከዘራፊዎቻቸው እጅ አዳናቸው። 49 የሳኦል ወንዶች ልጆች ዮናታን፥ የሱዊና ሜልኪሳ ነበሩ። የሁለቱ ሴቶች ልጆቹ ስም፥ የመጀመሪያ ልጁ ሜሮብና ታናሿ ሜልኮል ይባሉ ነበሩ። 50 የሳኦል ሚስት ስም አኪናሆም ነበር፥ እርሷም የአኪማአስ ልጅ ነበረች። የሠራዊቱ አዛዥ ስም፥ የሳኦል አጎት የኔር ልጅ አበኔር ነበር። 51 ቂስ የሳኦል አባት ነበር፤ የአበኔር አባት ኔርም የአቢኤል ልጅ ነበር። 52 በሳኦል ዘመን ሁሉ ከፍልስጥኤማውያን ጋር ከባድ ጦርነት ይካሄድ ነበር። ሳኦል ኃያል ወይም ብርቱ የሆነ ሰው ባየ ጊዜ ሁሉ ያንን ወደ ራሱ ይሰበስብ ነበር።



1 Samuel 14:1

አጠቃላይ መረጃ

ዮናታን በፍልስጥኤማውያን ሠራዊት ላይ ሁለተኛ ጥቃቱን ጀመረ፡፡

ወጣቱ ጋሻ ጃግሬው

የጌታውን የጦር መሣሪያዎች የመሸከም ኃላፊነት ያለበት ከአሥራ ሦሥት እስከ አሥራ ዘጠኝ ዓመት ባለ የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኝ ልጅ

የፍልስጥኤማውያን የጦር ካምፕ

ይህ የፍልስጥኤማውያን ሠራዊት የሰፈረበት የጦር ሰፈር ነው፡፡

1 Samuel 14:2

ጊብዓ

ይህ ከኢየሩሳሌም በስተሰሜን የሚገኝ የኮረብታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ከሮማኑ ዛፍ በታች

ፍሬው ወፍራም ሽፋን ያለው፣ ክብ፣ ቀይና የሚበሉ ብዙ ዘር የያዘ ዛፍ ነው

መጊዶን

መጊዶን ከኢየሩሳሌም በስተሰሜን የሚገኝ የቦታ ስም ነው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ስድስት መቶ ሰዎች ከእርሱ ጋር ነበሩ

"600 ሰዎች ከእርሱ ጋር ነበሩ' (ቁጥሮች ተመልከት)

የአኪጦብ ልጅ (የኢካቦድ ወንድም)

"አኪጦብ' እና "ኢካቦድ' የሰዎች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

የዔሊ ልጅ ፊንሐስ

ፊንሐስ ከካህናት አንዱ ነበር፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 1፡03 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

1 Samuel 14:4

ሌላኛውም ሾጣጣ ድንጋይ ሴኔ ይባል ነበረ

ይህ የሌላኛው ሾጣጣ ድንጋይ ስም ነበር፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ማክማስ … ጊብዓ

ከኢየሩሳሌም በስተሰሜን የሚገኙ ከተሞች (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 14:6

ወጣቱ ጋሻ ጃግሬው

የጌታውን የጦር መሣሪያዎች የመሸከም ኃላፊነት ያለበት ከአሥራ ሦሥት እስከ አሥራ ዘጠኝ ዓመት ባለ የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኝ ልጅ፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 14፡1 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

ወደ እነዚህ ቆላፋን (ያልተገረዙ)

ይህ አይሁድ ላልሆኑ ወንዶች ጥቅም ላይ የሚውል ክበረ ነክ ቃል ነው፡፡

በእኛ ፈንታ ይሠራ

"እኛን ለመደገፍ ይሠራ' ወይም "ይረዳን'

ምንም ነገር እግዚአብሔርን ከማዳን አያቆመውም

ይህ ድርብ አሉታዊ አሳብ በአዎንታዊ መልኩ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር ማዳን ይችላል' (ድርብ አሉታዊ ተመልከት)

በብዙ ወይም በጥቂት

እነዚህ ጥጎች በመካከል ያሉትን ነገሮች ሁሉ ያካትታሉ፡፡ አት፡- "በማንኛውም የሰው ቁጥር' (ስዕላዊ ንግግር ተመልከት)

በልብህ ያለውን ማንኛውንም ነገር

በዚህ ስፍራ ልብ የዮናታንን ፍልጎቶች ያመላክታል፡፡ አት፡- "ማድረግ የምትፈልገውን የትኛውንም ነገር' (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 14:8

ወደ እነርሱ አንወጣም

"ፍልስጥኤማውያን ወደ ሚገኙበት ወደ ሌላኛው የሸለቆ አቅጣጫ አንሄድም፡፡'

በእጃቸን አሳልፎ ሰጥቶአቸዋል

በዚህ ስፍራ እጅ እነርሱን ለማሸነፍ የሆነውን ኃይል ያመለክታል፡፡ አት፡- እነርሱን ለማሸነፍ ያስችለናል (ምትክ ቃል ተመልከት)

ይህ ምልክት ይሆነናል

"ይህ ጌታ ከእኛ ጋር እንደሆነ ያረጋግጥልናል'

1 Samuel 14:11

ለፍልስጥኤማውያን ጭፍራ ራሳቸውን ገለጡ

"የፍልስጥኤማውያን ወታደሮች እንዲያዩአቸው ፈቀዱ'

የጦር ሠፈር

የሠራዊት ከምፕ

ከተደበቁበት ጉድጓድ ይወጣሉ

ዕብራውያን እንደ እንሰሳ በጉድጓድ ውስጥ ተደብቀው እንደ ነበር ፍልሰጥኤማውያን አመልከቱ፡፡ (ዘይቤአዊ ንግግር ተመልከት)

አንድ ነገር እናሳያችኋለን

ይህ አንድ ትምህርት አስተምራችኋለሁ የሚል ትርጉም ያለው ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

በእስራኤል እጅ አሳልፎ ሰጣአቸው

በዚህ ስፍራ እጅ የሚለው የሚያመለክተው ፍልስጥኤማውያንን ለማሸነፍ የሆነውን ኃይል ነው፡፡ አትለ- እስራኤላውያን እንዲያሸንፉ አስቻላቸው፡፡ (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 14:13

ዮናታን በእጁና በእግሩ ወጣ

ይህን ያደረገው በጣም ከፍ ያለ ስለ ነበረ ነው፡፡ ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ አት፡- "በጣም ከፍ ያለ ስለ ነበረ ዮናታን እጆቹንና እግሮቹን በመጠቀም ወጣ' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ፍልስጥኤማውያን በዮናታን ተገደሉ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊደረግ ይቻላል፡፡ አት፡- "ዮናታን ፍልስጥኤማውያንን ገደለ' (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

ከእርሱ በኋላ ጋሻ ጃግሬው ጥቂቶችን ገደለ

"የዮናታን ጋሻ ጃግሬ ተከተለው የፍልስጥኤማውያንንም ወታደሮች ገደለ'

1 Samuel 14:15

በሰፈሩም በእርሻውና በሕዝቡም መካከል ሽብር ሆነ

ሽብር የሚለው የነገር ስም በማሰሪያ አንቀጽነት ወይም በቅጽልነት ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- "በሰፈርና በእርሻ የነበሩ የፍልስጥኤማውያን ወታደሮችና ከእነርሱ ጋር የነበረው ሕዝብ ሁሉ ተሸበሩ' ወይም "በሰፈርና በእርሻ የነበሩ የፍልስጥኤማውያን ወታደሮችና ከእነርሱ ጋር የነበረው ሕዝብ ሁሉ በጣም ፈሩ' (የነገር ስም ተመልከት)

ዘራፊዎች (አደጋ ጣዮች)

የእስራኤልን ከተሞች የሚዘርፉ ፍልስጥኤማውያን

ምድሪቱ ተናወጠች

ምክንያቱን መግልጽ ሊረዳ ይችላል፡፡ አት፡- "እግዚአብሔር ምድሪቱን አናወጣት' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 14:16

ጊብዓ

ይህቺ ሳኦል የተወለደባት ከተማ ነበረች፡፡ "ጊብዓ'ን በ1ሳሙኤል 10፡26 እንደተረጎምኸው ተርጉም፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

ወዲህና ወዲያ እየተራወጡ ተበታተኑ

እነዚህ ሁለት ሃረጎች ተመሳሳይ ትርጉም ይጋራሉ ወታደሮቹም በሁሉም አቅጣጫዎች ይሮጡ የነበረ በመሆኑ ላይ አጽንዖት ያደርጋሉ፡፡ (አጓዳኝነት ተመልከት)

1 Samuel 14:18

የእግዚአብሔርን ታቦት ወደዚህ አምጣ

ጥቂት ትርጉሞች በዚህ ስፍራ "የእግዚአብሔር ታቦት' በሚለው ምትክ "ኤፉድ' ይላሉ፡፡ (ልዩ ልዩ ትርጉሞች ተመልከት)

ግርግርታ

ትልቅ ድምጽና ትርምስምስ

እጅህን መልስ

ይህ "እያደረግህ ያለውን አቁም' የሚል ፈሊጣዊ ንግግር ይመስላል፡፡ እግዚአብሔርን ምሪት ለመጠየቅ አኪያ ታቦቱን እንዲጠቀም ሳኦል አልፈቀደም፡፡ አት፡- "በዚህ ጊዜ የተቀደሰውን ሰንዱቅ አታምጣ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 14:20

ከእርሱ ጋር የነበሩት ሕዝብ

ከሳኦል ጋር የቀሩ የእስራኤል ሠራዊት ቅሬታ

የእያንዳንዱ ፍልስጥኤማዊ ሰይፍ በባልንጀራው ላይ ነበረ

ሰይፎችን በሚመለከት ልክ ሕያዋን ሰዎች እንደሆኑ ተደርጎ ተነግሮአል፡፡ አት፡- "የፍልስጥኤም ወታደሮች እርስ በእርሳቸው በሰየፎቻቸው ተጠቃቁ' (ግዑዝ ነገርን እንደ ሰው ማየትን ተመልከት)

1 Samuel 14:22

በኮረብታዎቹ የተሸሸጉት የእስራኤል ሰዎች

ይህ ደፈጣን እያመለከተ አይደለም፡፡ እነዚህ ወታደሮች የተሸሸጉት ፍልስጥኤማውያንን ስለፈሩ ነበር፡፡ ይህ በግልጽ ሊቀመጥ ይችላል፡፡ አት፡- የፈሩ የእስራኤል ወታደሮች በኮረብታዎች ተሸሽገው ነበር፡፡ (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ቤትአዌን

ይህ በእስራኤል የሚገኝ ቦታ ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 13፡05 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡ (የስሞች አተረጓጎም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 14:24

ከወታደሮቹ ማንም ምግብ አልቀመሰም ነበር

ከሳኦል መሃላ የተነሣ ምንም መቅመስ እንዳልተፈቀደ ወታደሮቹ ተረድተው ነበር፡፡

ሕዝቡ ወደ ዱር ገባ

የፍልስጥኤም ወታደሮች ወደ ጫካ ሸሽተው ነበር የእስራኤል ወታደሮችም ወደዚያ ተከትለዋቸው ነበር፡፡

የሚፈስ ማር ነበር

በጫካ ውስጥ ምን ያህል ማር እንደነበር ለመግለጽ የተነገረ ግነት ነው፡፡ አት፡- "በሁሉ ሥፍራ በርካታ ማር ነበር' (ግነትና አጠቃላይነት ተመልከት)

ማንም እጁን ወደ አፉ አልዘረጋም

በዚህ ስፍራ የአንድ ሰው እጁን በአፉ ማድረጉ መብላትን የሚያሳይ ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "ማንም ምንም አልበላም' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ሕዝቡ መሐላውን ፈርቶ

ሕዝቡ ይፈሩ የነበረው መሐላውን ሳይሆን መሐላውን ከመስበር ጋር የተያያዘውን ቅጣት ነበር፡፡ አት፡- "ሕዝቡ መሐላውን ከሰበሩ ሳኦል የሚያደርግባቸውን ፈሩ' (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 14:27

አጠቃላይ መረጃ

ዮናታን የአባቱን መሐላ አወቀ፡፡

ሕዝቡን በመሐላ አሰራቸው

በዚህ ስፍራ መሐላን የመታዘዝ ግዴታን በሚመለከት ሕዝቡ በገመድ እንደታሰረ ዓይነት ተደርጎ ተነግሮአል፡፡ አት፡- "ሕዝቡ መሐላውን እንዲያከብር አዘዘ' (ዘይቤአዊ አነጋገር ተመልከት)

እጁን ወደ አፉ አደረገ

በዚህ ስፍራ እጁን ወደ አፉ የሚለው ለመብላት ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "ጥቂት ማር በላ' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ዓይኑ በራ

በረታ የሚል ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "እንደገና ብርታት አገኘ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

1 Samuel 14:29

ለምድሪቱ

የእስራኤልን ሕዝብ የሚወክል ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "ለእስራኤል' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ዓይኔ በራ

በረታ የሚል ፈሊጣዊ ንግግር ነው፡፡ አት፡- "እንደገና ብርታት አገኘ' (ፈሊጣዊ ንግግር ተመልከት)

ሕዝቡ ካገኙት … ምን ያህል የተሻለ

ሕዝቡ እንዲበላ ሊፈቀድለት ይገባ እንደነበር ለመግለጽ ዮናታን ይህንን በሁኔዎች ላይ የተደገፈ ጥያቄ ይጠቀማል፡፡ ይህ አሳብ ገላጭ ዐረፍተ ነገር ሊሆን ይችላል፡፡ አት፡- "ሕዝቡ ከጠላቶቻቸው የማረኩትን ዛሪ በነፃነት በልተው ቢሆን ኖሮ ድላችን የተሻለ ይሆን ነበር፡፡' (አሳብ ገላጭ ጥያቄና ሊሆኑ የሚችሉ ሁኔታዎች ተመልከት)

ምርኮ

ይህ ቃል ሕዝቡ ከጠላቶቻቸው ጋር በነበራቸው ጦርነት የወሰዷቸውን ነገሮች ያመለክታል፡፡

ስለዚህ አሁን ግድያው ታላቅ አልሆነም

በጦርነቱ ወቅቱ ወታደሮቹ ሊበሉ ስላልቻሉ፣ ቀኑ የረዘመውን ያህል እየደከሙ ሄዱ፡፡ ከዚህ የተነሣ ብዙ ፍልስጥኤማውያንን መግደል አልቻሉም፡፡

1 Samuel 14:31

አጠቃላይ መረጃ

የዮናታን ቃል ሠራዊቱን ከነበረባቸው ከፍተኛ ረሃብ የተነሣ እግዚአብሔርን እንዲበድሉ አደረጋቸው፡፡

ማክማስ

ይህ የቦታ ስም ነው፡፡ ይህንን በ1ሳሙኤል 13፡02 እንዴት እንደተረጎምህ ተመልከት፡፡

ኤሎን

በዛብሎን እስራኤል የሚገኝ ቦታ ነው (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ሕዝቡ

እስራኤላውያንን ያመለክታል፡፡

ከደማቸው ጋር በሉአቸው

በጣም ተርበው ስለነበር ከመብላታቸው በፊት ደሙን አላፈሰሱም ነበር፡፡ ይህ በሙሴ በኩል ለሕዝበ እሥራኤል የተሰጠውን ሕግ መተላለፍ ነበር፡፡ ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ አት፡- "በሕጉ እንደታዘዘው አስቀድመው ደማቸውን ሳያፈስሱ በሏቸው' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 14:33

ከደሙ ጋር በመብላታችሁ

ይህ በሙሴ በኩል ለሕዝበ እሥራኤል የተሰጠውን ሕግ መተላለፍ ነበር፡፡ ይህ ግልጽ ሊደረግ ይችላል፡፡ አት፡- "በሕጉ እንደታዘዘው አስቀድመው ደሙን ሳያፈስሱ ሥጋ በመብላታቸው'

በታማኝነት አላደረጋችሁም

ሁሉም ወታደር ታማኝነቱን ስላላጓደለ ሳኦል ሠራዊቱን ሁሉ በታማኝነት እንዳላደረገ መክሰሱ አጠቃላይ ፍረጃ ነው፡፡ (ግነትና አጠቃላይነት ተመልከት)

አሁን ትልቅ ድንጋይ አንከባላችሁ አቅርቡልኝ

ድንጋዩ እንሰሳቱን ከፍ አድርጎ ስለሚይዝ ደማቸውን ማፍሰስን ቀላል ያደርገዋል በዚህ እረዱና ብሉ ይህ ሳኦልን ደሙ ከእንሰሳው በተገቢ ሁኔታ ተወግዶ መሆኑን ለማየት ያስችለዋል፡፡

1 Samuel 14:35

አጠቃላይ መረጃ

ሕዝቡ ለማረድና ለመብላት እንሰሳቶቻቸውን ወደ ትልቁ ደንጋይ እንዲያመጡ ሳኦል ነገራቸው፡፡

ሳኦል ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሠራ

ሳኦል ይህን መሠዊያ የሠራው ሕዝቡ በ1ሳሙኤል 14፡33 ወደ እርሱ ካመጡለት ትልቅ ድንጋይ ይሁን ግልጽ አይደለም፡፡

1 Samuel 14:36

አጠቃለይ መረጃ

ሳኦል ከፍልስጥኤማውያን ጋር የነበረውን ጦርነት ለመቀጠል ፈልጓል፡፡

ከመካከላቸው አንድ እንኳ በሕይወት እንዲኖር አንተው

ለግድያው አጽንዖት ለመስጠት ይህ በአሉታዊ መንገድ ተገልጾአል፡፡ በአዎንታዊ መልኩም ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- "እያንዳንዳቸውን እንግደል' (ምጸት ተመልከት)

ደስ የሚያሰኝህን ሁሉ አድርግ

ጦርነቱን ለመቀጠል ሳኦል የሠራዊቱን ድጋፍ አግኝቶአል፡፡

ወደ እግዚአብሔር እንቅረብ

በዚህ ስፍራ "ወደ እግዚአብሔር መቅረብ' እርሱን ምክር ከመጠየቅ ጋር ተያይዟል፡፡ አት፡- "ምን ማደረግ እንዳለብን እግዚአብሔርን እንጠይቅ' (ምትክ ቃል ተመልከት)

በእስራኤል እጅ አሳልፈህ ትሰጣቸዋለህን?

በዚህ ስፍራ "እጅ' እነርሱን ለማሸነፍ የሚሆንን ኃይል ያመለክታል፡፡ አት፡-"እንድናሸንፋቸው አስችለን' (ምትክ ቃል ተመልከት)

በዚያን ቀን ግን እግዚአብሔር አልመለሰለትም

ይህ እግዚአብሔር ሳኦልን ለመርዳት ፈቃደኛ እንዳልሆነ ያመላክታል፡፡

1 Samuel 14:38

ሕዝቡ

ይህ እስራኤላውያንን ያመልከታል

ዛሬ ይህ ኃጢአት በምን እንደሆነ እወቁ

"ኃጢአት የሠራውን እወቁ'

በልጄ በዮናታን ቢሆን ፈጽሞ ይሞታል

ሳኦል ዮናታን በደለኛ እንደሆነ ስላላመነ ይህንን ሊሆን እንደ ሚችል ሁኔታ አድርጎ ገለጸ፡፡ (ሊሆን የሚችል ሁኔታ ተመልከት)

ከሕዝቡም አንድ የመለሰለሰት ሰው አልነበረም

አብዛኛዎቹ ዮናታን የሳኦልን መሐላ እንደሰበረ ስለሚያውቁ ዝም አሉ፡፡ ይህ በግልጽ ሊቀመጥ ይችላል፡፡ አት፡- "ሰዎቹ በደለኛው ማን እንደነበረ ያውቁ ነበር ነገር ግን ማናቸውም ለሳኦል ምንም አላሉም፡፡' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

1 Samuel 14:40

እስራኤልንም ሁሉ … አለ

በዚያ የነበሩት የእስራኤል ወታደሮች ብቻ ስለሆኑ ይህ አጠቃላይነት ነው፡፡ አት፡- "በዚያ ለነበሩት የእስራኤል ወታደሮች እንዲህ አለ' (ግነትና አጠቃላይነት ተመልከት)

ቱሚም ስጠን

በዚያን ጊዜ እስራኤላውያን ከእግዚአብሔር ምሪት ለመቀበል ኡሪምና ቱሚም የተባሉ የተለዩ ድንጋዮች ይጠቀሙ ነበር፡፡ አት፡- "በቱሚም አማካይነት አስታውቀን' (እንደሚታወቅ ታሳቢ የተደረገ እውቀትና ግልጽ ያልተደረገ መረጃ ተመልከት)

ቱሚም

ይህ ከመጀመሪያ ቋንቋ በትውስት የተወሰደ ነው፡፡ (ቅጂ ወይም ትውስት ቃላት ተመልከት)

ሳኦልና ዮናታን በዕጣው ተለዩ፣ ሕዝቡ ግን ነፃ ሆነ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይቻላል፡፡ አት፡- ዕጣዎቹ ዮናታን ወይም ሳኦል በደለኞች እንደሆኑ ነገር ግን ሠራዊቱ በደለኛ እንዳልሆነ አመለከቱ (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

ከዚያም ዮናታን በዕጣው ተለየ

ይህ በአድራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- ከዚያም ዕጣው ዮናታን በደለኛ እንደሆነ አመለከተ (አድራጊና ተደራጊ ማሰሪያ አንቀጽ ተመልከት)

1 Samuel 14:43

አጠቃላይ መረጃ

ዕጣው ዮናታን ኃጢአት እንዳደረገ አሳየ፡፡

ያደረግኸውን ንገረኝ

"እንዴት ኃጢአት እንዳደረግህ ንገረኝ' ወይም "ያደረግኸው ስሕተት ምን እንደሆነ ንገረኝ'

እሞታለሁ

ሊሆኑ የሚችሉ ትርጉሞች 1) "ለመሞት ፈቃደኛ ነኝ' ወይም 2) "ያንን ስላደረግሁ በሞት ልቀጣ ይገባኛል'

እግዚአብሔር እንዲህ ያድርግብኝ እንዲህም ይጨምርብኝ፤ ዮናታን ሆይ ፈጽም ትሞታለህ

ከአንድ ቀን ባነሰ ጊዜ ውስጥ ሳኦል ትርጉም የሌለው መሐላ አደረገ፡፡ አት፡- ዮናታን፣ ካልገደልኩህ እግዚአብሔር ይግደለኝ

1 Samuel 14:45

አጠቃላይ መረጃ

ሠራዊቱ ከሳኦል ለዮናታን ተከላከለ ጠበቀውም፡፡

በውኑ ለእስራኤል ይህን ታላቅ ድል ያደረገ ዮናታን ይሞታልን? ይህ አይሁን!

ሕዝቡ ሳኦልን ገሰፀ፡፡ ይህ አሳብ ገላጭ ጥያቄ በገላጭ አባባል ሊተረጎም ይችላል፡፡ አት፡- ዮናታን ይህን ታላቅ ድል ለእስራኤል አድርጓል፡፡ በእርግጥ ዮናታን አይሞትም፡፡ (አሳብ ገላጭ ጥያቄ ተመልከት)

ሕያው እግዚአብሔርን

ሕዝቡ በዮናታን ላይ አንዳች ነገር እንዲሆን አንዳማየፈቅዱ ቁርጠኛነታቸውን እየገለጹ ነበር፡፡

ከራሱ ጠጉር አንዲት በምድር ላይ አትወድቅም

ይህ ግነት የእስራኤል ሕዝብ እንዴት ዮናታንን እንደሚጠብቁትና ደህንነቱን እንደሚከታተሉ ያሳያል፡፡ ይህ ምፀት በአዎንታዊ መልኩ ሊገለጽ ይችላል፡፡ አት፡- ከየትኛውም ጉዳት እንጠብቀዋለን (ግነትና አጠቃላይነት እና ምፀት ተመልከት)

1 Samuel 14:47

አጠቃላይ መረጃ

ለአጭር ጊዜ ሳኦል በታላቅ ድፍረት የእስራኤላውያንን ጠላቶች በማሸነፍ አገልግሏል፡፡

እስራኤል

ይህ የእስራኤልን ሕዝብ የሚወክል ምትክ ቃል ነው፡፡ አት፡- "እስራኤላውያን' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ሞዓብ

ይህ የሞዓብ ሕዝብን ያመለክታል፡፡ አት፡- "ሞዓባውያን' (ምትክ ቃል ተመልከት)

ዔዶም

ይህ የዔዶም ሰዎችን ያመለክታል፡፡ አት፡- "ዔዶማውያን' (ምትክ ቃል ተመልከት)

በየሄደበትም ሁሉ

"ሠራዊቱን በላከበት ሥፍራ ሁሉ'

ከ …እጅ

እጅ የሚለው ቃል ቁጥጥርን ይወክላል፡፡ አት፡- "ከ … ቁጥጥር' (ምትክ ቃል ተመልከት)

1 Samuel 14:49

አጠቃላይ መረጃ

ይህ በሳኦል ቤተሰብ ዙሪያ ታሪካዊ ዳራ ነው፡፡

የሱዊ … ሜልኪሳ

እነዚህ የወንዶች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

ሜሮብ … ሜልኮል

አነዚህ የሴቶች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

አኪናሆም … አኪማአስ

እነዚህ የሴቶች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

አቤኔር … ኔር … ቂስ … አቢኤል

እነዚህ የወንዶች ስሞች ናቸው፡፡ (የስሞች አተረጓገም መንገድ ተመልከት)

1 Samuel 14:52

በሳኦልም እድሜ ሁሉ

"በሳኦል የሕይወት ዘመን ሁሉ'


Chapter 15

1 ሳሙኤልም ሳኦልን እንዲህ አለው፥”እግዚአብሔር በሕዝቡ በእስራኤል ላይ ንጉሥ ትሆን ዘንድ እንድቀባህ ላከኝ። አሁንም የእግዚአብሔርን ቃል ስማ። 2 የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር የሚለው እንዲህ ነው፥ 'እስራኤል ከግብፅ በወጣ ጊዜ አማሌቅ እየተቃወመ በመንገዱ ላይ ያደረገበትን አስታውሻለሁ። 3 አሁንም ሂድና አማሌቅን ምታ፥ ያላቸውን ሁሉ ፈጽመህ ደምስስ። አትራራላቸው፥ ወንድና ሴቱን፥ ልጅና ሕፃኑን፥ በሬና በጉን፥ ግመልና አህያውን ግደል።" 4 ሳኦል ሕዝቡን በጥላኢም ከተማ ሰብስቦ ቆጠራቸው፤ እነርሱም ሁለት መቶ ሺህ እግረኞችና ዐሥር ሺህ የይሁዳ ሰዎች ነበሩ። 5 ከዚያም ሳኦል ወደ አማሌቅ ከተማ መጥቶ በሸለቆው ውስጥ አደፈጠ። 6 ከዚያም ሳኦል ቄናውያንን፥ "ከግብፅ በመጡ ጊዜ ለእስራኤል ሕዝብ በሙሉ ደግነትን አሳይታችኋልና ከእነርሱ ጋር እንዳላጠፋችሁ፥ ከአማሌቃውያን መካከል ተለይታችሁ ውጡና ሂዱ" አላቸው። ስለዚህ ቄናውያን ከአማሌቃውያን ተለይተው ሄዱ። 7 ሳኦልም አማሌቃውያንን ከኤውላጥ ጀምሮ ከግብፅ በስተምሥራቅ እስካለችው እስከ ሱር ድረስ መታቸው። 8 የአማሌቃውያኑን ንጉሥ አጋግን ከነሕይወቱ ያዘው፤ ሕዝቡን ሁሉ በሰይፍ ስለት ፈጽሞ አጠፋቸው። 9 ነገር ግን ሳኦልና ሕዝቡ አጋግን፥ እንዲሁም ምርጥ የሆኑትን በጎች፥ በሬዎች፥ የሰቡትን ጥጆችና የበግ ጠቦቶች በሕይወት ተዉአቸው። መልካም የሆነውን ሁሉ አላጠፉም። የተናቀውንና ዋጋ ቢስ የሆነውን ነገር ሁሉ ግን ፈጽመው ደመሰሱ። 10 ከዚያም የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ ሳሙኤል መጣ፥ 11 "እኔን ከመከተል ስለተመለሰና ያዘዝኩትንም ስላልፈጸመ ሳኦልን በማንገሤ ተጸጽቻለሁ"። ሳሙኤልም ተቆጣ፤ ሌሊቱን በሙሉ ወደ እግዚአብሔር ሲጮህ አደረ። 12 ሳሙኤልም ሳኦልን በጠዋት ለመገናኘት ማልዶ ተነሣ። ለሳሙኤልም፥ "ሳኦል ወደ ቀርሜሎስ መጥቶ ለራሱ ሐውልት አቆመ፥ ከዚያም ተመልሶ ወደ ጌልገላ ወረደ" ብለው ነገሩት። 13 ከዚያም ሳሙኤል ወደ ሳኦል መጣ፥ ሳኦልም፥ "አንተ በእግዚአብሔር የተባረክህ ነህ! የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ፈጽሜአለሁ" አለው። 14 ሳሙኤልም፥ "ታዲያ ይህ በጆሮዬ የምሰማው የበጎች ድምፅና የበሬዎች ግሣት ምንድነው?" አለው። 15 ሳኦልም፥ "ከአማሌቃውያኑ ያመጧቸው ናቸው። ሕዝቡ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ለመሠዋት ምርጥ የሆኑትን በጎችና በሬዎች በሕይወት አስቀሯቸው። የቀሩትን ፈጽመን አጥፍተናል" ብሎ መለሰለት። 16 ከዚያም ሳሙኤል ሳኦልን፥ "አድምጠኝ፥ በዛሬው ሌሊት እግዚአብሔር የነገረኝን እነግርሃለሁ" አለው። ሳኦልም፥ "ተናገር!" አለው። 17 ሳሙኤልም እንዲህ አለው፥ "በራስህ ግምት ታናሽ ብትሆንም በእስራኤል ነገዶች ላይ አለቃ ተደረግህ። እግዚአብሔርም በእስራኤል ላይ ንጉሥ አድርጎ ቀባህ፤ 18 እግዚአብሔርም፥ 'ሂድና ኃጢአተኞቹን አማሌቃውያንን ፈጽመህ አጥፋቸው፥ እስኪጠፉም ድረስ ተዋጋቸው' ብሎ በመንገድህ ልኮህ ነበር። 19 ታዲያ የእግዚአብሔርን ድምፅ ያልታዘዝከው ለምንድነው? ከዚያ ይልቅ ግን ከምርኮው በመውሰድ በእግዚአብሔር ፊት ክፋትን አደረግህ።" 20 ሳኦልም ሳሙኤልን፥ "የእግዚአብሔርን ድምፅ በትክክል ታዝዣለሁ፥ እግዚአብሔር በላከኝም መንገድ ሄጃለሁ። የአማሌቅን ንጉሥ አጋግን ማርኬዋለሁ፥ አማሌቃውያንንም በሙሉ ፈጽሜ ደምስሻለሁ። 21 ሕዝቡ ግን ከምርኮው ላይ ጥቂት በጎችንና በሬዎችን፥ ሊጠፉም የነበሩ ምርጥ ነገሮችን ለአምላክህ ለእግዚአብሔር በጌልገላ ሊሠዉአቸው ወሰዱ" አለው። 22 ሳሙኤልም፥ "የእግዚአብሔርን ድምፅ ከመታዘዝ የበለጠ በሚቃጠል መባና መሥዋዕት እግዚአብሔር ደስ ይሰኛል? ከመሥዋዕት መታዘዝ ይሻላል፥ ከአውራ በግ ስብም መስማት ይሻላል። 23 እምቢተኝነት እንደ ምዋርተኝነት ኃጢአት ነው፥ እልኸኝነትም እንደ አመጸኝነትና እንደ ክፋት ነው። የእግዚአብሔርን ቃል ንቀሃልና እርሱም ደግሞ ንጉሥ እንዳትሆን ንቆሃል“ አለው። 24 ከዚያም ሳኦል ሳሙኤልን፥”ኃጢአትን ሠርቻለሁ፤ ሕዝቡን ስለፈራሁና ቃላቸውን ስለታዘዝኩ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝና የአንተን ቃል ተላልፌአለሁ። 25 አሁንም እባክህን ኃጢአቴን ይቅር በለኝ፥ ለእግዚአብሔር እንድሰግድም ከእኔ ጋር ተመለስ“ አለው። 26 ሳሙኤልም ሳኦልን፥”ከአንተ ጋር አልመለስም፤ የእግዚአብሔርን ቃል ንቀሃልና አንተም በእስራኤል ላይ ንጉሥ እንዳትሆን እግዚአብሔር ንቆሃል" አለው። 27 ሳሙኤል ለመሄድ ዘወር ባለ ጊዜ፥ ሳኦል የልብሱን ጫፍ ያዘ፥ እርሱም ተቀደደ። 28 ሳሙኤልም፥ "እግዚአብሔር ዛሬ የእስራኤልን መንግሥት ከአንተ ቀደደው፥ ከአንተ ለሚሻለው ለጎረቤትህም አሳልፎ ሰጠው። 29 ደግሞም የእስራኤል ኃይል አይዋሽም፥ አሳቡንም አይለውጥም፥ እርሱ አሳቡን መለወጥ ይችል ዘንድ ሰው አይደለምና“ አለው። 30 ከዚያም ሳኦል፥”ኃጢአትን አድርጌአለሁ። አሁን ግን እባክህ በሕዝቤ ሽማግሌዎችና በእስራኤል ፊት አክብረኝ። ለአምላክህ ለእግዚአብሔር እንድሰግድ ከእኔ ጋር ተመለስ“ አለው። 31 ስለዚህ ሳሙኤል ከሳኦል ኋላ ተመለሰ፥ ሳኦልም ለእግዚአብሔር ሰገደ። 32 ከዚያም ሳሙኤል፥”የአማሌቃውያንን ንጉሥ አጋግን አምጡልኝ“ አለ። አጋግ በሠንሠለት አንደታሠረ ወደ እርሱ መጣና፥”ለካስ ሞት እንዲህ መራራ ነው“ አለ። 33 ሳሙኤልም፥”ሰይፍህ እናቶችን ልጅ ዐልባ እንዳደረጋቸው አሁን እናትህ በሴቶች መካከል ልጅ ዐልባ ትሆናለች“ ብሎ መለሰለት። ከዚያም ሳሙኤል አጋግን በእግዚአብሔር ፊት በጌልገላ ቆራረጠው። 34 ሳሙኤል ወደ ራማ ሄደ፥ ሳኦልም ወደ ቤቱ ወደ ሳኦል ጊብዓ ሄደ። 35 ሳሙኤል እስከሞተበት ጊዜ ድረስ ሳኦልን አላየውም፥ ለሳኦልም አለቀሰለት። እግዚአብሔርም ሳኦልን በእስራኤል ላይ በማንገሡ አዘነ።



Chapter 16

1 እግዚአብሔርም ሳሙኤልን፥ “በእስራኤል ንጉሥ እንዳይሆን ለናቅኩት ለሳኦል የምታለቅስለት እስከ መቼ ነው? በወንዶች ልጆቹ መካከል ለራሴ ንጉሥ የሚሆነውን መርጫለሁና ወደ ቤተ ልሔማዊው ወደ እሴይ እልክሃለሁ። የዘይት መያዣ ቀንድህን በዘይት ሞልተህ ሂድ” አለው። 2 ሳሙኤልም፥ “እንዴት መሄድ እችላለሁ? ሳኦል ከሰማ ይገድለኛል” አለ። እግዚአብሔርም፥ “አንዲት ጊደር ይዘህ ሂድና፥ 'ለእግዚአብሔር ልሠዋ መጥቻለሁ' በል። 3 እሴይንም ወደ መሥዋዕቱ ጥራው፥ እኔም የምታደርገውን አሳይሃለሁ። የምነግርህንም እርሱን ትቀባልኛለህ” አለው። 4 ሳሙኤልም እግዚአብሔር እንደተናገረው አደረገ፥ ወደ ቤተ ልሔምም ሄደ። የከተማይቱም ሽማግሌዎች እየተንቀጠቀጡ ሊገናኙት መጡና፥ “በሰላም ነው የመጣኸው?” አሉት። 5 እርሱም፥ “በሰላም ነው። ለእግዚአብሔር ልሠዋ መጥቻለሁ። ራሳችሁን ለእግዚአብሔር ቀድሱና ከእኔ ጋር ወደ መሥዋዕቱ ኑ”አላቸው። እሴይንና ወንዶች ልጆቹንም ቀደሳቸው፥ ወደ መሥዋዕቱም ጠራቸው። 6 እነርሱ በመጡ ጊዜም፥ ወደ ኤልያብ ተመልክቶ እግዚአብሔር የሚቀባው በእርግጥ በፊቱ ቆሟል ብሎ በልቡ አሰበ። 7 ነገር ግን እግዚአብሔር ሳሙኤልን፥ "እኔ ንቄዋለሁና ውጫዊ ገጽታውን ወይም የቁመቱን ዘለግታ አትመልከት። እግዚአብሔር ሰው እንደሚያይ አያይምና፤ ሰው ውጫዊ ገጽታን ያያል፥ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል" አለው። 8 ከዚያም እሴይ አሚናዳብን ጠርቶ በሳሙኤል ፊት እንዲያልፍ አደረገው። ሳሙኤልም፥ "እግዚአብሔር ይኸኛውንም አልመረጠውም“ አለ። 9 ከዚያም እሴይ ሳማን አሳለፈው። ሳሙኤልም፥ "እግዚአብሔር ይኸኛውንም አልመረጠውም“ አለ። 10 እሴይ ሰባቱን ወንዶች ልጆቹን በሳሙኤል ፊት እንዲያልፉ አደረጋቸው። ሳሙኤልም እሴይን፥”እግዚአብሔር ከእነዚህ አንዳቸውንም አልመረጠም“ አለው። 11 ሳሙኤልም እሴይን፥”ወንዶቹ ልጆችህ እነዚህ ብቻ ናቸው? “ አለው። እርሱም፥”የሁሉ ታናሽ የሆነው ገና ቀርቷል፥ እርሱ ግን በጎች እየጠበቀ ነው" ብሎ መለሰ። ሳሙኤልም እሴይን፥ "ልከህ አስመጣው፤ እርሱ እዚህ እስኪመጣ ድረስ አንቀመጥምና" አለው። 12 እሴይም ልኮ አስመጣው። በመጣ ጊዜም ልጁ ቀይ፥ ዐይኖቹ የተዋቡና መልከ መልካም ገጽታ ነበረው። እግዚአብሔርም፥ "ያ ሰው እርሱ ነውና ተነሣ፤ ቀባውም" አለው። 13 ሳሙኤልም የዘይቱን ቀንድ አንሥቶ በወንድሞቹ መካከል እርሱን ቀባው። ከዚያን ቀን ጀምሮ የእግዚአብሔር መንፈስ በእርሱ ላይ በኃይል መጣበት። ሳሙኤልም ተነሥቶ ወደ አርማቴም ሄደ። 14 የእግዚአብሔር መንፈስ ከሳኦል ተለየ፥ በምትኩም ከእግዚአብሔር የታዘዘ ክፉ መንፈስ አሠቃየው። 15 የሳኦል አገልጋዮችም፥ "ተመልከት፥ ክፉ መንፈስ ከእግዚአብሔር ዘንድ እያሠቃየህ ነው። 16 ደህና አድርጎ በገና መደርደር የሚችል ሰው እንዲፈልጉ ጌታችን በፊቱ ያሉትን አገልጋዮቹን ይዘዝ። ከዚያም ከእግዚአብሔር ዘንድ ክፉ መንፈስ በሆነብህ ጊዜ እርሱ ይጫወትልሃል፥ አንተም ደኅና ትሆናለህ" አሉት። 17 ሳኦልም አገልጋዮቹን፥ "በገና በደንብ መደርደር የሚችል ሰው ፈልጋችሁ አምጡልኝ" አላቸው። 18 ከዚያም ከወጣቶቹ አንዱ እንዲህ ሲል መለሰ፥ "ደኅና አድርጎ በገና መደርደር የሚችለውን፥ ጽኑ፥ ኃያል፥ ተዋጊ፥ በንግግሩ ጠንቃቃና መልከ መልካም የሆነውን የቤተ ልሔማዊውን የእሴይን ልጅ አይቻለሁ፥ እግዚአብሔርም ከእርሱ ጋር ነው።" 19 ስለዚህ ሳኦል መልዕክተኞችን ወደ እሴይ ልኮ፥ "ከበጎች ጋር ያለውን ልጅህን ዳዊትን ላክልኝ" አለው። 20 እሴይም እንጀራና ወይን ጠጅ የተሞላ አቁማዳ የተጫነበትን አህያ፥ ከፍየል ጠቦት ጋር አስይዞ ልጁን ዳዊትን ወደ ሳኦል ላከው። 21 ከዚያም ዳዊት ወደ ሳኦል መጣና አገልግሎቱን መስጠት ጀመረ። ሳኦል እጅግ ወደደው፥ ዳዊትም ጋሻ ጃግሬው ሆነ። 22 ሳኦልም፥ "በዐይኔ ፊት ሞገስን አግኝቷልና ዳዊት በፊቴ እንዲቆም ፈቃድህ ይሁን“ ብሎ ወደ እሴይ ላከ። 23 በሳኦል ላይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ክፉ መንፈስ በሚሆንበት ጊዜ ሁሉ ዳዊት በገና አንሥቶ ይደረድርለት ነበር። ስለዚህ ሳኦል ይታደስና ደኅና ይሆን ነበር፥ ክፉውም መንፈስ ከእርሱ ይርቅ ነበር።



Chapter 17

1 ፍልስጥኤማውያን ሠራዊታቸውን ለውጊያ አዘጋጁ። እነርሱም የይሁዳ በሆነችው በሰኮት ተሰበሰቡ። በሰኮትና በዓዜቃ መካከል በምትገኘው በኤፌስደሚምም ሰፈሩ። 2 ሳኦልና የእስራኤል ሰዎችም ተሰብስበው በኤላ ሸለቆ ሰፈሩ፥ ፍልስጥኤማውያንን ለመግጠምም ስፍራቸውን ያዙ። 3 ፍልስጥኤማውያን በአንደኛው ወገን ተራራ ላይ ቆሙ፥ በዚህኛው ወገን ባለው ተራራ ላይ እስራኤላውያኑ ቆሙ፥ በመካከላቸውም ሸለቆ ነበር። 4 የጌት ሰው ጎልያድ የሚባል አንድ ጀግና ከፍልስጥኤማውያን የጦር ሰፈር ወጣ፥ ቁመቱም ስድስት ክንድ ከስንዝር ነበር። 5 በራሱ ላይ ከነሐስ የተሠራ የራስ ቁር ደፍቶ፥ ጥሩርም ለብሶ ነበር። ጥሩሩም አምስት ሺህ የነሐስ ሰቅል ይመዝን ነበር። 6 በእግሮቹ ላይ የነሐስ ገምባሌዎች አድርጎ ነበር፥ በትከሻዎቹም መሓል ቀለል ያለ የነሐስ ጦር ነበር። 7 የጦሩ ዘንግ እንደ ሸማኔ መጠቅለያ ወፍራም ነበር። የጦሩ ጫፍ ስድስት መቶ የብረት ሰቅል ይመዝን ነበር። ጋሻ ጃግሬው በፊቱ ሄደ። 8 እርሱም ተነሥቶ በእስራኤል ሠልፈኞች ላይ እንዲህ በማለት ጮኸ፥ “ለውጊያ የተሰለፋችሁት ለምንድነው? እኔ ፍልስጥኤማዊ፥ እናንተ የሳኦል አገልጋዮች አይደላችሁም? ለራሳችሁ አንድ ሰው ምረጡና ወደ እኔ ይውረድ። 9 እርሱ ሊዋጋኝ ቢችልና ቢገድለኝ እኛ አገልጋዮቻችሁ እንሆናለን። ነገር ግን ባሸንፈውና ብገድለው እናንተ አገልጋዮቻችን በመሆን ታገለግሉናላችሁ።” 10 ፍልስጥኤማዊው ደገመና፥ “ዛሬ የእስራኤልን ሰልፈኞች እገዳደራቸዋለሁ። እንድንዋጋ አንድ ሰው ስጡኝ" አለ። 11 ፍልስጥኤማዊው የተናገረውን ሳኦልና እስራኤላውያን ሁሉ በሰሙ ጊዜ እጅግ ፈሩ፥ ተስፋም ቆረጡ። 12 ዳዊት በይሁዳ የሚኖረው የቤተ ልሔም ኤፍራታዊው የእሴይ ልጅ ነበር። እሴይ ስምንት ወንዶች ልጆች ነበሩት። በሳኦል ዘመን እሴይ በዕድሜው ያረጀና ከወንዶቹ ሁሉ በዕድሜ የገፋ ሰው ነበር። 13 የእሴይ ሦስቱ ታላላቅ ልጆች ሳኦልን ተከትለው ወደ ጦርነቱ ሄደው ነበር። ወደ ጦርነት የሄዱት የሦስቱ ወንዶች ልጆች ስም፥ የመጀመሪያው ልጅ ኤልያብ፥ ተከታዩ አሚናዳብና ሦስተኛው ሣማ ይባሉ ነበር። 14 ዳዊት የሁሉም ታናሽ ነበር። ትልልቆቹ ሦስቱ ሳኦልን ተከተሉት። 15 ዳዊት በሳኦል ሠራዊትና በቤተ ልሔም የሚገኙትን የአባቱን በጎች በመጠበቅ ተግባር ወዲያና ወዲህ ይመላለስ ናበር። 16 ፍልስጥኤማዊው ኃያል ሰው ለአርባ ቀናት በየጠዋቱና በየምሽቱ ለጦርነት ዝግጁ መሆኑን ለማሳየት ይቀርብ ነበር። 17 ከዚያም እሴይ ልጁን ዳዊትን እንዲህ አለው፥”ከዚህ ከተጠበሰው እሸት ዐሥር ኪሎና እነዚህን ዐሥር ዳቦዎች በጦር ሰፈሩ ውስጥ ላሉት ወንድሞችህ ፈጥነህ ውሰድላቸው። 18 በተጨማሪም እነዚህን ዐሥር የአይብ ጥፍጥፎች ለሻለቃቸው ስጠው። ወንድሞችህ ያሉበትን ሁኔታ ተመልከትና ደኅና ስለመሆናቸው ማረጋገጫ አምጣልኝ። 19 ወንድሞችህ ከሳኦልና ከእስራኤል ሰዎች ሁሉ ጋር ፍልስጥኤማውያንን እየተዋጉ በኤላ ሸለቆ ናቸው።“ 20 ዳዊት ማልዶ ተነሣና በጎቹን ለእረኛ ዐደራ ሰጠ። እርሱም እሴይ እንዳዘዘው የወንድሞቹን ስንቅ ይዞ ሄደ። ሠራዊቱ ወደ ውጊያው ግምባር እየፎከረ በመውጣት ላይ እያለ ዳዊት ወደ ጦር ሰፈሩ ደረሰ። 21 እስራኤላውያንና ፍልስጥኤማውያን፥ ሠራዊት በሠራዊት ላይ ለውጊያ ተሰለፉ። 22 ዳዊት የያዘውን ዕቃ ለስንቅ ጠባቂው ዐደራ ሰጥቶ ወደ ሠራዊቱ በመሮጥ ለወንድሞቹ ሰላምታ አቀረበ። 23 ከእነርሱ ጋር እየተነጋገረ እያለ ጎልያድ ተብሎ የሚጠራው፥ ከጌት የመጣው ፍልስጥኤማዊ ከሰልፈኞች መካከል ወጥቶ የቀድሞውን የሚመስል ቃል ተናገረ። ዳዊትም ሰማቸው። 24 የእስራኤል ሰዎች ሁሉ ሰውዬውን ባዩት ጊዜ፥ ከእርሱ ሸሹ፥ እጅግም ፈርተውት ነበር። 25 የእስራኤልም ሰዎች፥ "ይህን የሚወጣውን ሰው አያችሁት? እስራኤልን ለመገዳደር ነው የመጣው። እርሱን የሚገድለውን ሰው ንጉሡ እጅግ ያበለጽገዋል፥ ልጁን ይድርለታል፥ የአባቱንም ቤት በእስራኤል ውስጥ ከግብር ነጻ ያደርጋቸዋል" ይባባሉ ነበር። 26 ዳዊትም በአጠገቡ የቆሙትን ሰዎች፥ "ይህንን ፍልስጥኤማዊ ለሚገድልና ከእስራኤል ኀፍረትን ለሚያስወግድ ሰው ምን ይደረግለታል? የሕያው እግዚአብሔርን ሠራዊት ሊንቅ ይህ ያልተገረዘ ፍልስጥኤማዊ ማን ሆነና ነው?" አላቸው። 27 ከዚያም ሰዎቹ ቀደም ሲል የተናገሩትን ደግመው፥ "ስለዚህ እርሱን ለሚገድለው የሚደረግለት ይህ ነው" አሉት። 28 ዳዊት ከሰዎቹ ጋር ሲነጋገር የሁሉ ታላቅ የሆነው ወንድምየው ኤልያብ ሰማው። ኤልያብም በዳዊት ላይ ቁጣው ነድዶ፥ "ወደዚህ የወረድከው ለምንድነው? እነዚያንስ ጥቂት በጎች በምድረ በዳ ውስጥ ለማን ተውካቸው? እኔ ትዕቢትህንና የልብህን ክፋት አውቃለሁ፤ ወደዚህ የወረድከው ውጊያውን ለማየት ነውና" አለው። 29 ዳዊትም፥ "አሁን እኔ ምን አደረኩ? እንዲያው መጠየቄ ብቻ አልነበረም?" አለው። 30 ከእርሱ ወደ ሌላው ዞር ብሎ በተመሳሳይ መንገድ ተናገረ። ሰዎቹም የቀድሞውን የሚመስል መልስ ሰጡት። 31 ዳዊት የተናገረው ቃል በተሰማ ጊዜ፥ ወታደሮች ቃሉን ለሳኦል ነገሩት፥ እርሱም ዳዊትን አስጠራው። 32 ከዚያም ዳዊት ሳኦልን፥ "በዚያ ፍልስጥኤማዊ ምክንያት የማንም ልብ አይውደቅ፤ አገልጋይህ ሄዶ ከፍልስጥኤማዊው ጋር ይዋጋል" አለው። 33 ሳኦልም ዳዊትን፥ "አንተ ከዚህ ፍልስጥኤማዊ ጋር ለመዋጋት መሄድ አትችልም፤ አንተ ገና ልጅ ነህ፥ እርሱ ደግሞ ከወጣትነቱ ጀምሮ ተዋጊ ነው" አለው። 34 ዳዊት ግን ሳኦልን፥ "አገልጋይህ የአባቴን በጎች እጠብቅ ነበር። አንበሳ ወይም ድብ መጥቶ ከመንጋው ጠቦት በሚወስድበት ጊዜ 35 በኋላው ተከትዬ እመታውና ከአፉ አስጠለው ነበር። ሊያጠቃኝ በተነሣብኝ ጊዜም ጉሮሮውን ይዤ እመታውና እገድለው ነበር። 36 አገልጋይህ አንበሳና ድብ ገድያለሁ። የሕያው እግዚአብሔርን ሠራዊት ስለተገዳደረ ይህም ያልተገረዘ ፍልስጥኤማዊ ከእነርሱ እንደ አንዱ ይሆናል" አለው። 37 ዳዊትም፥ "እግዚአብሔር ከአንበሳና ከድብ መዳፍ አድኖኛል። ከዚህም ፍልስጥኤማዊ እጅ ያድነኛል" አለው። 38 ከዚያም ሳኦል ዳዊትን፥ "ሂድ፥ እግዚአብሔርም ከአንተ ጋር ይሁን" አለው። ሳኦል የራሱን የጦር መሣሪያ ለዳዊት አስታጠቀው። በራሱ ላይ የነሐስ ቁር ደፋለት፥ ጥሩርም አለበሰው። 39 ዳዊትም ሰይፉን በጦር ልብሱ ላይ ታጠቀው። ነገር ግን አልተለማመደውምና ለመራመድ አቃተው። ከዚያም ዳዊት ሳኦልን፥ "አልተለማመድኳቸውምና በእነዚህ መዋጋት አልችልም" አለው። ስለዚህ ዳዊት ከላዩ ላይ አወለቃቸው። 40 በትሩን በእጁ ያዘ፥ ከጅረቱም አምስት ድቡልቡል ድንጋዮች መርጦ በእረኛ ኮሮጆው ውስጥ ጨመራቸው። ፍልስጥኤማዊውን በሚቀርብበት ጊዜ ወንጭፉን ይዞ ነበር። 41 ፍልስጥኤማዊውም በፊት ለፊቱ ከሚሄደው ጋሻ ጃግሬው ጋር መጥቶ ወደ ዳዊት ቀረበ። 42 ፍልስጥኤማዊው ዙሪያውን ሲመለከት ዳዊትን ባየው ጊዜ ቀይ፥ መልከ መልካም ገጽታ ያለው ትንሽ ልጅ ብቻ ስለነበረ ናቀው። 43 ፍልስጥኤማዊው ዳዊትን፥ "በትር ይዘህ የምትመጣብኝ እኔ ውሻ ነኝ?" አለው። ፍልስጥኤማዊውም በአማልክቶቹ ስም ዳዊትን ረገመው። 44 ፍልስጥኤማዊውም ዳዊትን፥ "ወደ እኔ ና፥ እኔም ሥጋህን ለሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት እሰጣለሁ" አለው። 45 ዳዊትም ለፍልስጥኤማዊው እንዲህ ሲል መለሰለት፥ "አንተ ሰይፍ፥ ጦርና ጭሬ ይዘህ ትመጣብኛለህ። እኔ ግን አንተ ባቃለልከው፥ የእስራኤል ሠራዊት አምላክ በሆነው፥ በእግዚአብሔር ስም እመጣብሃለሁ። 46 ዛሬ እግዚአብሔር በአንተ ላይ ድልን ይሰጠኛል፥ እገድልሃለሁ፥ ራስህንም ከሰውነትህ ላይ አነሣዋለሁ። ዛሬ የፍልስጥኤምን ሠራዊት ሬሳ ለሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት እሰጣለሁ፥ ይኸውም ምድር ሁሉ በእስራኤል አምላክ እንዳለ እንዲያውቅና 47 በዚህ የተሰበሰበው ሁሉ እግዚአብሔር በሰይፍ ወይም በጦር ድልን እንደማይሰጥ እንዲያውቁ ነው። ጦርነቱ የእግዚአብሔር ነውና እናንተንም በእጃችን ላይ አሳልፎ ይሰጣችኋል።" 48 ፍልስጥኤማዊው ተነሥቶ ዳዊትን በቀረበው ጊዜ ዳዊት ሊገናኘው ወደ ጠላት ጦር በፍጥነት ሮጠ። 49 ዳዊት እጁን ወደ ኮሮጆው አስገብቶ አንድ ድንጋይ ከዚያ ወሰደ፥ ወነጨፈውና የፍልስጥኤማዊውን ግንባር መታው። ድንጋዩም በፍልስጥኤማዊው ግንባር ውስጥ ጠልቆ ገባ፥ እርሱም በግንባሩ በምድር ላይ ተደፋ። 50 ዳዊት ፍልስጥኤማዊውን በወንጭፍና በድንጋይ አሸነፈው። ፍልስጥኤማዊውንም መትቶ ገደለው። በዳዊት እጅ ሰይፍ አልነበረም። 51 ከዚያም ዳዊት ሮጠና በፍልስጥኤማዊው ላይ ቆመ፥ ከእርሱም ሰይፉን ወሰደ፥ ከሰገባው አወጣና ገደለው፥ በእርሱም ራሱን ቆርጦ አነሣው። ፍልስጥኤማውያን ጀግናቸው መሞቱን ባዩ ጊዜ ሸሹ። 52 ከዚያም የእስራኤልና የይሁዳ ሰዎች እልል እያሉ ተነሥተው ፍልስጥኤማውያንን እስከ ሸለቆውና እስከ ኤቅሮን መግቢያ ድረስ አሳደዷቸው። የፍልስጥኤማውያኑ ሬሳ ከሸዓራይም እስከ ጌትና ዔቅሮን ድረስ በየመንገዱ ወድቆ ነበር። 53 የእስራኤል ሰዎች ፍልስጥኤማውያንን ከማሳደድ ተመለሱና የጦር ሰፈራቸውን በዘበዙ። 54 ዳዊት የፍልስጥኤማዊውን ራስ ወስደ፥ ወደ ኢየሩሳሌምም አመጣው፥ የጦር መሣሪያውን ግን በድንኳኑ ውስጥ አኖረው። 55 ዳዊት ፍልስጥኤማዊውን ለመጋጠም ሲሄድ ሳኦል ባየው ጊዜ፥ የሰራዊቱን አዛዥ አበኔርን፥ "አንተ አበኔር፥ ይህ ወጣት የማን ልጅ ነው?" አለው። አበኔርም፥ "ንጉሥ ሆይ፥ በሕያውነትህ እምላለሁ፥ አላውቅም" አለው። 56 ንጉሡም፥ "የማን ልጅ እንደሆነ ምናልባት ሊያውቁት የሚችሉትን ጠይቅ" አለው። 57 ዳዊት ፍልስጥኤማዊውን ገድሎ በተመለሰ ጊዜ፥ አበኔር ወሰደው፥ የፍልስጥኤማዊውን ራስ በእጁ እንደያዘ ወደ ሳኦል አመጣው። 58 ሳኦልም፥ "አንተ ወጣት፥ የማን ልጅ ነህ?" አለው። ዳዊትም፥ "እኔ የቤተ ልሔማዊው የአገልጋይህ የእሴይ ልጅ ነኝ" ብሎ መለሰለት።



Chapter 18

1 ለሳኦል መናገሩን በጨረሰ ጊዜ የዮናታን ነፍስ በዳዊት ነፍስ ታሰረች፥ ዮናታንም እንደ ራሱ ነፍስ አድርጎ ወደደው። 2 በዚያ ቀን ሳኦል ዳዊትን ወደ ራሱ አገልግሎት ወሰደው፤ ወደ አባቱ ቤት እንዲመለስ አላሰናበተውም። 3 ዮናታን ዳዊትን እንደ ራሱ ነፍስ አድርጎ ስለወደደው በመካከላቸው የወዳጅነት ቃል ኪዳን አደረጉ። 4 ዮናታን የለበሰውን ካባ አውልቆ ከጦር ልብሱ ጋር፥ እንዲሁም ሰይፉን፥ ቀስቱንና መታጠቂያውን ለዳዊት ሰጠው። 5 ዳዊት ሳኦል ወደሚልከው ቦታ ሁሉ ይሄድ ነበር፥ ይከናወንለትም ነበር። ሳኦልም በተዋጊዎቹ ላይ ሾመው። ይህም በሕዝቡ ዓይን ሁሉ ደግሞም በሳኦል አገልጋዮች ፊት ደስ የሚያሰኝ ሆነ። 6 ፍልስጥኤማውያንን ድል አድርገው ወደ መኖሪያቸው በመመለስ ላይ እያሉ ከእስራኤል ከተሞች ሁሉ ንጉሥ ሳኦልን ለመገናኘት፥ ሴቶች በከበሮና በሙዚቃ መሳሪያዎች በደስታ እየዘመሩና እየጨፈሩ መጡ። 7 ሴቶቹም ሲጫወቱ እየተቀባበሉ ይዘምሩ ነበር፤ እነርሱም፥ "ሳኦል ሺዎችን ገደል፥ ዳዊትም ዐሥር ሺዎችን ገደለ" እያሉ ዘመሩ። 8 ሳኦል እጅግ ተቆጣ፥ ይህም መዝሙር አስከፋው። እርሱም፥ "ለዳዊት ዐሥር ሺዎች አሉ፥ ለእኔ ግን ሺዎችን ብቻ። ታዲያ ከመንግሥት በቀር ምን ቀረው?" አለ። 9 ሳኦል ከዚያን ቀን ጀምሮ ዳዊትን በጥርጣሬ ዐይን ተመለከተው። 10 በቀጣዩ ቀን በሳኦል ላይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ክፉ መንፈስ መጣበት። እርሱም በቤት ውስጥ እንደ ዕብድ ይለፈልፍ ነበር። ስለዚህ ዳዊት በየቀኑ ያደርግ እንደነበረው በገናውን ይደረድር ነበር። ሳኦልም በእጁ ጦር ይዞ ነበር። 11 ሳኦል፥ "ዳዊትን ከግድግዳው ጋር አጣብቀዋለሁ" ብሎ በማሰብ ጦሩን ወረወረበት። ነገር ግን ዳዊት ከሳኦል ፊት ሁለት ጊዜ እንዲህ ባለ መንገድ አመለጠ። 12 እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር እንጂ ከእርሱ ጋር ስላልነበረ ሳኦል ዳዊትን ፈራው። 13 ስለዚህ ሳኦል ከፊቱ አራቀው፥ ሻለቃም አድርጎ ሾመው። በዚህ ሁኔታ ዳዊት በሕዝቡ ፊት ይወጣና ይገባ ነበር። 14 እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ስለነበረ ዳዊት የሚሠራው ሁሉ ይከናወንለት ነበር። 15 እንደ ተከናወነለት ሳኦል ባየ ጊዜ እጅግ ፈራው። 16 ነገር ግን በፊታቸው ይወጣና ይገባ ስለነበረ እስራኤልና ይሁዳ ሁሉ ዳዊትን ወደዱት። 17 ከዚያም ሳኦል ዳዊትን፥ "ትልቋ ልጄ ሜሮብ ይቹት። እርሷን እድርልሃለሁ። ብቻ ጎብዝልኝ፥ የእግዚአብሔርን ጦርነቶችም ተዋጋ" አለው። ሳኦል፥ "እጄ በእርሱ ላይ አይሁን፥ ነገር ግን የፍልስጥኤማውያን እጅ በእርሱ ላይ ይሁን" ብሎ አስቦአልና። 18 ዳዊትም ሳኦልን፥ "የንጉሥ አማች ለመሆን እኔ ማነኝ? ሕይወቴ ወይም የአባቴ ቤተ ሰብ በእስራኤል ውስጥ ምንድነው?" አለው። 19 ነገር ግን የሳኦል ልጅ ሜሮብ ለዳዊት የምትዳርበት ጊዜ ሲደርስ ለመሓላታዊው ለኤድሪኤል ተዳረች። 20 ነገር ግን የሳኦል ልጅ ሜልኮል ዳዊትን ወደደችው። ለሳኦል ነገሩት፥ ይህም እርሱን ደስ አሰኘው። 21 ከዚያም ሳኦል፥ "ወጥመድ እንድትሆነውና የፍልስጥኤማውያን እጅ በእርሱ ላይ እንድትሆን እርሷን እድርለታለሁ" ብሎ አሰበ። ስለዚህ ሳኦል ዳዊትን ለሁለተኛ ጊዜ፥ "አማቼ ትሆናለህ" አለው። 22 ሳኦል አገልጋዮቹን እንዲህ ሲል አዘዛቸው፥ "ዳዊትን በምስጢር እንዲህ በሉት፥ 'አስተውል፥ ንጉሡ በአንተ ደስ ብሎታል፥ አገልጋዮቹም ሁሉ ይወዱሃል። እንግዲያው የንጉሡ አማች ሁን'" 23 ስለዚህ የሳኦል አገልጋዮች ይህንን ቃል ለዳዊት ነገሩት። ዳዊትም፥ "እኔ ድሃና ብዙም የማልታወቅ ሰው ሆኜ እያለሁ የንጉሥ አማች እንድሆን ማሰባችሁ ጉዳዩ እንዴት ቀልሎ ታያችሁ?" አላቸው። 24 የሳኦል አገልጋዮችም ዳዊት የተናገረውን ቃል ነገሩት። 25 ሳኦልም፥ "ለዳዊት እንዲህ ትሉታላችሁ፥ 'የንጉሡን ጠላቶች ለመበቀል ከአንድ መቶ የፍልስጥኤማውያን ሸለፈት ብቻ በቀር ንጉሡ ምንም ጥሎሽ አይፈልግም"። ዳዊት በፍልስጥኤማውያን እጅ እንዲወድቅ ለማድረግ ሳኦል አሰበ። 26 አገልጋዮቹ ይህንን ቃል ለዳዊት በነገሩት ጊዜ የንጉሡ አማች መሆን ዳዊትን ደስ አሰኘው። 27 እነዚያ ቀናት ከማብቃታቸው በፊት፥ ዳዊት ከሰዎቹ ጋር ሄዶ ሁለት መቶ ፍልስጥኤማውያንን ገደለ። ዳዊት የንጉሡ አማች ይሆን ዘንድ ሸለፈቶቹን አመጣ፥ ለንጉሡም ሙሉውን ቁጥር አስረከቡ። ስለዚህ ሳኦል ልጁን ሜልኮልን ዳረለት። 28 እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር እንደነበረ ሳኦል አየ፥ ዐወቀም። የሳኦል ልጅ ሜልኮልም ወደደችው። 29 ሳኦልም ዳዊትን የበለጠ ፈራው። ሳኦል የዳዊት ጠላቱ እንደሆነ ቀጠለ። 30 ከዚያም የፍልስጥኤም ልዑላን ብዙ ጊዜ ያደርጉት እንደነበረው ለጦርነት መጡ፥ ዳዊት ከሳኦል አገልጋዮች ሁሉ በበለጠ ሁኔታ የተሳካለት ሆነ፥ በመሆኑም ስሙ እጅግ የተከበረ ሆነ።



Chapter 19

1 ሳኦል ልጁን ዮናታንን እና አገልጋዮቹን በሙሉ ዳዊትን እንዲገድሉት ነገራቸው። የሳኦል ልጅ ዮናታን ግን ዳዊትን እጅግ ይወድደው ነበር። 2 ስለዚህ ዮናታን ዳዊትን፥ "አባቴ ሳኦል ሊገድልህ ይፈልጋል። በመሆኑም ለራስህ ጥንቃቄ አድርግ፥ በነገውም ቀን በምስጢራዊ ቦታ ተደበቅ። 3 አንተ ባለህበት አካባቢ ሄጄ በአባቴ አጠገብ እቆማለሁ፥ ስለ አንተም አነጋግረዋለሁ። አንዳች ነገር ካገኘሁኝም እነግርሃለሁ“ አለው። 4 ዮናታንም ለአባቱ ለሳኦል ስለ ዳዊት መልካምን ነገር ተናገረ፥ እንዲህም አለው፥”ንጉሡ በአገልጋዩ በዳዊት ላይ ክፉ ነገር አያድርግ። እርሱ ክፉ አላደረገብህም፥ እርሱ የሠራው ሥራ ለአንተ መልካም ሆኖልሃልና። 5 ነፍሱን በእጁ ላይ ጥሎ ፍልስጥኤማዊውን ገደለ። እግዚአብሔርም ለእስራኤል በሙሉ ታላቅ ድልን ሰጠ። አንተም አይተህ ደስ ብሎህ ነበር። ያለምንም ምክንያት ዳዊትን በመግደልህ በንጹህ ደም ላይ ለምን ኃጢአት ትሠራለህ?“ 6 ሳኦልም ዮናታንን ሰማው። ሳኦልም፥”ሕያው እግዚአብሔርን! ዳዊት አይገደልም“ ብሎ ማለ። 7 ከዚያም ዮናታን ዳዊትን ጠራው፥ ዮናታንም ይህንን ነገር ሁሉ ነገረው። ዮናታንም ዳዊትን ወደ ሳኦል አመጣው፥ እርሱም እንደቀድሞው በፊቱ ነበረ። 8 እንደገናም ጦርነት ሆነ። ዳዊት ወጥቶ ከፍልስጥኤማውያን ጋር ተዋጋ፥ በታላቅ አገዳደልም ድል አደረጋቸው። እነርሱም ከፊቱ ሸሹ። 9 ሳኦል በእጁ ጦሩን እንደያዘ በቤቱ ተቀምጦ እያለ ክፉ መንፈስ ከእግዚአብሔር ዘንድ በሳኦል ላይ መጣበት፥ ዳዊትም በገና ይደረድር ነበር። 10 ሳኦል በጦሩ ዳዊትን ከግድግዳው ጋር ለማጣበቅ ሞከረ፥ ዳዊት ግን ከሳኦል ፊት ዘወር አለ፥ ስለዚህ የሳኦል ጦር በግድግዳው ላይ ተሰካ። በዚያ ምሽት ዳዊት ሸሽቶ አመለጠ። 11 ሳኦልም በማግስቱ ይገድለው ዘንድ ከብበው እንዲጠብቁት ወደ ዳዊት ቤት መልዕክተኞች ላከ። የዳዊት ሚስት ሜልኮልም፥”በዚህ ሌሊት ሕይወትህን ካላዳንክ ነገ መገደልህ ነው“ አለችው። 12 ስለዚህ ሜልኮል ዳዊትን በመስኮት እንዲወርድ አደረገችው። እርሱም ሄደ፥ ሸሽቶም አመለጠ። 13 ሜልኮልም የቤተሰቡን የጣዖት ምስል ወስዳ በአልጋው ውስጥ አጋደመችው። በራስጌው ከፍየል ጸጉር የተሠራ ትራስ አስቀመጠች፥ በልብስም ሸፈነችው። 14 ሳኦል ዳዊትን የሚወስዱ መልዕክተኞች በላከ ጊዜ እርሷ፥ "አሞታል" አለቻቸው። 15 ከዚያም ሳኦል ዳዊትን እንዲያዩት መልዕክተኞች ላከ፥ እርሱም፥ "እንድገድለው ከነዐልጋው አምጡልኝ" አላቸው። 16 መልዕክተኞቹ ወደ ቤት በገቡ ጊዜ፥ በዐልጋው ውስጥ የቤተሰቡ የጣዖት ምስል፥ በራስጌውም ከፍየል ጸጉር የተሠራው ትራስ ነበር። 17 ሳኦል ሜልኮልን፥ "ጠላቴ እንዲሄድና እንዲያመልጥ በማድረግ ለምን አታለልሽኝ?" አላት። ሜልኮልም ለሳኦል፥ "'ልሂድ፥ አለበለዚያ እገድልሻለሁ' ስላለኝ ነው" ብላ መለሰችለት። 18 ዳዊትም ሸሽቶ አመለጠ፥ ሳሙኤል ወዳለበት ወደ ራማም ሄደ፥ ሳኦል ያደረገበትንም ሁሉ ነገረው። ከዚያም እርሱና ሳሙኤል ሄዱ፥ በነዋትም ተቀመጡ። 19 ለሳኦልም፥ "ዕወቀው፥ ዳዊት በራማ ነዋት ነው" ተብሎ ተነገረው። 20 ሳኦልም ዳዊትን እንዲይዙት መልዕክተኞችን ላከ። እነርሱም ትንቢት የሚናገሩ የነቢያትን ጉባዔ፥ ሳሙኤልንም መሪያቸው ሆኖ ባዩ ጊዜ በሳኦል መልዕክተኞች ላይ የእግዚአብሔር መንፈስ መጣባቸው፥ እነርሱም ደግሞ ትንቢት ተናገሩ። 21 ይህ ሁኔታ ለሳኦል በተነገረው ጊዜ፥ ሌሎች መልዕክተኞችን ላከ፥ እነርሱም ደግሞ ትንቢት ተናገሩ። ስለዚህ ሳኦል እንደገና ለሦስተኛ ጊዜ ሌሎች መልዕክተኞችን ላከ፥ እነርሱም ደግሞ ትንቢት ተናገሩ። 22 ከዚያም እርሱ ደግሞ ወደ አርማቴም ሄደ፥ በሤኩ ወዳለው ጥልቅ የውሃ ጉድጓድም መጣ። እርሱም፥”ሳሙኤልና ዳዊት የት ነው ያሉት? “ ብሎ ጠየቀ። አንደኛው ሰው፥”በራማ ነዋት ናቸው“ ብሎ መለሰለት። 23 ሳኦልም በራማ ወዳለው ነዋት ሄደ። የእግዚአብሔር መንፈስ በእርሱም ላይ መጣ፥ በራማም ወደሚገኘው ወደ ነዋት እስኪደርስ ድረስ በመንገድ ላይ ትንቢት ይናገር ነበር። 24 እርሱም ደግሞ ልብሶቹን አወለቀ፥ በሳሙኤል ፊት እርሱም ደግሞ ትንቢት ተናገረ፥ ያን ቀንና ሌሊቱን ሁሉ ራቁቱን ተጋደመ። እነርሱም፥”ሳኦል ከነቢያት አንዱ ሆነ እንዴ? “ ያሉት በዚህ ምክንያት ነው።



Chapter 20

1 ከዚያም ዳዊት በራማ ካለው ከነዋት ሸሽቶ መጣና ዮናታንን፥”ምን አድርጌአለሁ? ጥፋቴስ ምንድነው? በአባትህ ፊት ኃጢአቴ ምን ቢሆን ነው ሕይወቴን ለማጥፋት የሚፈልገው? “ አለው። 2 ዮናታንም ዳዊትን፥”ይህ ከአንተ ይራቅ፥ አትሞትም። ነገሩ ትልቅም ይሁን ትንሽ ሳይነግረኝ አባቴ ምንም አያደርግም። አባቴ ይህንን ነገር ለምን ይደብቀኛል? ነገሩ እንዲህ አይደለም። 3 ዳዊት ግን እንደገና ማለና፥ “በፊትህ ሞገስ ማግኘቴን አባትህ ያውቃል። እርሱም፥ 'ይህንን ዮናታን አይወቅ፥ ካልሆነ ያዝናል' ይላል። በሕያው እግዚአብሔር ስም፥ በሕያው ነፍስህም እምላለሁ፥ በእኔና በሞት መካከል የቀረው አንድ እርምጃ ነው" አለው። 4 ዮናታን ዳዊትን፥ "የምትጠይቀኝን ሁሉ አደርግልሃለሁ" አለው። 5 ዳዊትም ዮናታንን፥ "ነገ አዲስ ጨረቃ የምትታይበት ቀን ነው፥ ከንጉሡ ጋር ለመብላት መቀመጥ ይኖርብኛል። እስከ ሦስተኛው ቀን ምሽት ድረስ በመስኩ ውስጥ ሄጄ እንድደበቅ ፍቀድልኝ" አለው። 6 አባትህ እኔን በማጣቱ ከጠየቀህ፥ "ዳዊት፥ መላው ቤተ ሰቡ ዓመታዊ መሥዋዕት ስለሚያቀርቡ ወደ ቤተ ልሔም ይሄድ ዘንድ እንድፈቅድለት አጥብቆ ለመነኝ' በለው። 7 እርሱም፥ 'መልካም ነው' ካለህ ነገሩ ለአገልጋይህ ሰላም ሆኗል ማለት ነው። ነገር ግን እርሱ እጅግ ከተቆጣ ክፉ ሊያደርግብኝ እንደወሰነ በዚህ ታውቃለህ። 8 እንግዲህ አገልጋይህን በርኅራኄ ተመልከተኝ። በእግዚአብሔር ፊት ከአገልጋይህ ጋር ቃል ኪዳን አድርገሃልና። ኃጢአት ቢገኝብኝ ግን አንተው ግደለኝ፤ ለምንስ ወደ አባትህ ትወስደኛለህ?" አለው። 9 ዮናታንም፥ "ይህ ከአንተ ይራቅ! አባቴ ክፉ ሊያደርግብህ መወሰኑን ባውቅ አልነግርህም?" 10 ዳዊትም ዮናታንን፥ "አባትህ አንደ አጋጣሚ በቁጣ ቢመልስልህ ማን ይነግረኛል?" አለው። 11 ዮናታንም ዳዊትን፥ "ና፥ ወደ መስኩ እንሂድ" አለው። ሁለቱም ወደ መስኩ ሄዱ። 12 ዮናታንም ዳዊትን እንዲህ አለው፥ "የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ምስክር ይሁን። ነገ ወይም በሦስተኛው ቀን እንደዚህ ባለው ሰዓት አባቴን በምጠይቀው ጊዜ፥ ስለ ዳዊት በጎ አሳብ ካለው ልኬብህ አላሳውቅህም? 13 አባቴ በአንተ ላይ ክፉ ማድረጉ የሚያስደስተው ከሆነ በሰላም እንድትሄድ ባላሳውቅህና ባላሰናብትህ እግዚአብሔር በዮናታን ላይ ይህንን እና ከዚህም የከፋውን ያድርግበት። ከአባቴ ጋር እንደነበረ እግዚአብሔር ከአንተም ጋር ይሁን። 14 አንተስ በሕይወት በምኖርበት ዘመን እንዳልሞት የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታማኝነት አታሳየኝም? 15 እግዚአብሔር የዳዊትን ጠላቶች፥ እያንዳንዳቸውን ከምድር ላይ በሚያጠፋበት ጊዜ የቃል ኪዳን ታማኝነትህን ከቤቴ አታጥፋ"። 16 ሰለዚህ ዮናታን ከዳዊት ቤት ጋር ቃል ኪዳን አደረገና”እግዚአብሔር ከዳዊት ጠላቶች እጅ ይጠይቀው“ አለ። 17 ዮናታን ነፍሱን እንደሚወዳት ዳዊትን ይወደው ስለነበረ፥ ለእርሱ ከነበረው ፍቅር የተነሣ ዳዊት እንደገና እንዲምልለት አደረገ። 18 ከዚያም ዮናታን እንዲህ አለው፥”ነገ አዲስ ጨረቃ የምትታይበት የወር መጀመሪያ ቀን ነው። ወንበርህ ባዶ ስለሚሆን ላትኖር ነው። 19 ለሦስት ቀናት ከቆየህ በኋላ፥ ፈጥነህ ውረድና በዚህ ጉዳይ ካሁን በፊት ወደተደበቅህበት ስፍራ መጥተህ በኤዜል ድንጋይ አጠገብ ቆይ። 20 በዒላማ ላይ የምወረውር መስዬ ሦስት ፍላጻዎችን ወደዚያ አቅራቢያ እወረውራለሁ። 21 ከእኔ ጋር ያለውን ታዳጊ ወጣት እልከውና፥ 'ሂድ ፍላጻዎቹን ፈልግ' እለዋለሁ። ታዳጊውን ልጅ፥ 'ተመልከት፥ ፍላጻዎቹ አጠገብህ ናቸው፤ ውሰዳቸው' ካልኩት ሕያው እግዚአብሔርን! ለአንተ ደኅንነት እንጂ ጉዳት አይሆንብህምና ትመጣለህ። 22 ነገር ግን ታዳጊውን ወጣት፥ 'ተመልከት፥ ፍላጻዎቹ ከአንተ በላይ ናቸው' ካልኩት እግዚአብሔር አሰናብቶሃልና መንገድህን ሂድ። 23 እኔና አንተ ያደረግነውን ስምምነት በሚመለከት እግዚአብሔር በእኔና በአንተ መካከል ለዘላለም ምስክር ነው።" 24 ስለዚህ ዳዊት በመስኩ ውስጥ ተደበቀ። አዲስ ጨረቃ በሆነ ጊዜ ንጉሡ ምግብ ለመብላት ተቀመጠ። 25 ንጉሡ እንደተለመደው በግድግዳው አጠገብ በነበረው በመቀመጫው ላይ ተቀመጠ። ዮናታን ተነሣ፥ አበኔርም በሳኦል አጠገብ ተቀምጦ ነበር። የዳዊት ቦታ ግን ባዶ ነበር። 26 በዚያን ቀን ሳኦል ገና ምንም አልተናገረም፥ ምክንያቱም፥ "አንድ ነገር ደርሶበት ይሆናል፥ ወይም በሕጉ መሰረት አልነጻም ይሆናል፤ በርግጥ ባይነጻ ነው" ብሎ ሳላሰበ ነው። 27 ነገር ግን አዲስ ጨረቃ በታየችበት ማግስት፥ በሁለተኛው ቀን የዳዊት ስፍራ ባዶ ነበር። ሳኦል ልጁን ዮናታንን፥ "የእሴይ ልጅ ዳዊት ትላንትም ይሁን ዛሬ ወደ ማዕድ ያልመጣው ለምንድነው?" አለው። 28 ዮናታንም ለሳኦል እንዲህ በማለት መለሰለት፥ "ዳዊት ወደ ቤተ ልሔም ለመሄድ እንድፈቅድለት አጥብቆ ለመነኝ። 29 እርሱም፥ 'እባክህን እንድሄድ ፍቀድልኝ። በዚያ ከተማ ቤተሰባችን የሚያቀርበው መሥዋዕት አለ፥ እኔም በዚያ እንድገኝ ወንድሜ አዞኛል። አሁንም በፊትህ ሞገስን ካገኘሁ፥ ወንድሞቼን አያቸው ዘንድ እንድሄድ እባክህን ፍቀድልኝ' አለኝ። ወደ ንጉሡ ማዕድ ያልመጣው በዚህ ምክንያት ነው።" 30 ከዚያም የሳኦል ቁጣ በዮናታን ላይ ነደደ፥ እርሱም እንዲህ አለው፥ "አንተ የጠማማና አመጸኛ ሴት ልጅ! ለራስህ ኃፍረትና ለእናትህ የዕርቃንነት ኃፍረት የእሴይን ልጅ እንደ መረጥክ የማላውቅ መሰለህ? 31 የእሴይ ልጅ በምድር ላይ እስካለ ድረስ አንተም ሆንክ መንግሥትህ አትጸኑም። አሁንም በእርግጥ መሞት የሚገባው ነውና ልከህ አስመጣልኝ።“ 32 ዮናታንም አባቱን ሳኦልን፥”የሚገደለው በምን ምክንያት ነው? ያደረገውስ ምንድነው? “ ሲል መለሰለት። 33 በዚያን ጊዜ ሳኦል ሊገድለው ጦሩን ወረወረበት። ስለዚህ አባቱ ዳዊትን ለመግደል መወሰኑን ዮናታን ተረዳ። 34 ዮናታን እጅግ ተቆጥቶ ከማዕድ ተነሣ፥ አባቱ ስላዋረደው ስለ ዳዊት አዝኖ ነበርና በወሩ በሁለተኛው ቀን ምንም ምግብ አልበላም። 35 በማግስቱ ዮናታን ከዳዊት ጋር ወደተቀጣጠሩበት መስክ ሄደ፥ አንድ ታዳጊ ወጣትም አብሮት ነበር። 36 እርሱም ታዳጊውን ወጣት፥”ሩጥ፥ የምወረውራቸውን ፍላጻዎች ሰብስብ“ አለው። ታዳጊው ወጣት በሚሮጥበት ጊዜ ፍላጻውን ከበላዩ ላይ ወረወረው። 37 ታዳጊው ወጣት ዮናታን የወረወረው ፍላጻ ወደ ወደቀበት ስፍራ በደረሰ ጊዜ፥ ዮናታን ታዳጊውን ተጣርቶ፥ "ፍላጻው ከአንተ በላይ ነው" አለው። 38 ዮናታንም ታዳጊውን፥ "ቶሎ በል፥ ፍጠን፥ አትዘግይ!" አለው። ስለዚህ የዮናታኑ ታዳጊ ወጣት ፍላጻዎቹን ሰብስቦ ወደ ጌታው መጣ። 39 ታዳጊው ወጣት ግን አንዳች የሚያውቀው አልነበረም። ጉዳዩን የሚያውቁት ዮናታንና ዳዊት ብቻ ነበሩ። 40 ዮናታን የጦር መሣሪያዎቹን ለታዳጊው ወጣት ሰጥቶ፥ "ሂድ፥ ወደ ከተማ ውሰዳቸው" አለው። 41 ታዳጊው ወጣት እንደ ሄደ፥ ዳዊት ከጉብታው ኋላ ተነሣ፥ ወደ ምድርም ተጎንብሶ ሦስት ጊዜ ሰገደ። እርስ በእርሳቸው ተሳሳሙ፥ ተላቀሱም፥ ዳዊትም አብዝቶ አለቀሰ። 42 ዮናታንም ዳዊትን፥”'እግዚአብሔር፥ በእኔና በአንተ፥ በዘሬና በዘርህ መካከል ለዘላለም ይሁን' ተባብለን በእግዚአብሔር ስም ተማምለናልና በሰላም ሂድ” አለው። ከዚያም ዳዊት ተነሥቶ ሄደ፥ ዮናታንም ወደ ከተማ ተመለሰ።



Chapter 21

1 ከዚያም ዳዊት ካህኑን አቢሜሌክን ለማግኘት ወደ ኖብ መጣ። አቢሜሌክም ዳዊትን ለመገናኘት እየተንቀጠቀጠ መጣና፥ “አንድም ሰው አብሮህ ያልሆነውና ብቻህን የሆንከው ለምንደነው?” አለው። 2 ዳዊትም ካህኑን አቢሜሌክን፥ “ንጉሡ ለአንድ ጉዳይ ልኮኛል። እርሱም፥ 'ስለምልክህ ጉዳይና ያዘዝኩህን ነገር ማንም እንዳያውቅ'ብሎኛል። ወጣቶቹንም የሆነ ቦታ ላይ እንዲጠብቁኝ ነግሬአቸዋለሁ። 3 ታዲያ አሁን እጅህ ላይ ምን አለ? አምስት እንጀራ ወይም ያለውን ነገር ስጠኝ” አለው። 4 ካህኑም ለዳዊት መልሶ፥ “ማንኛውም ሰው የሚበላው እንጀራ የለኝም፥ ነገር ግን ታዳጊ ወጣቶቹ ራሳቸውን ከሴቶች ጠብቀው ከሆነ የተቀደሰ እንጀራ አለ” አለው። 5 ዳዊትም ለካህኑ እንዲህ ሲል መለሰለት፥ “በእርግጥ በእነዚህ ሦስት ቀናት ከሴቶች ተጠብቀናል። ለተራ ተልዕኮ በሚወጡበት ጊዜ ራሳቸውን ካነጹ ለዚህ ተልዕኮማ ከእኔ ጋር ያሉት ወጣቶች ሰውነት ለእግዚአብሔር እንዴት የበለጠ የተቀደሰ አይሆንም?” 6 ስለዚህ ከተነሣ በኋላ በስፍራው ትኩስ እንጀራ ይደረግ ዘንድ፥ ከእግዚአብሔር ፊት ከተነሣው፥ ከገጸ ሕብስቱ በስተቀር ሌላ እንጀራ በዚያ አልነበረምና፥ ካህኑ ለእግዚአብሔር የተቀደሰውን እንጀራ ሰጠው። 7 በዚያም ቀን ከሳኦል አገልጋዮች አንዱ በእግዚአብሔር ፊት በእዚያ ቆይቶ ነበር፤ ስሙ ዶይቅ የሚባል ኤዶማዊ፥ የሳኦል የእረኞቹ አለቃ ነበር። 8 ዳዊት አቢሜሌክን፥ "እዚህ ጦር ወይም ሰይፍ ይኖርሃል? የንጉሡ ጉዳይ አስቸኳይ ስለነበረ ሰይፌንም ሆነ መሣሪያዬን ይዤ አልመጣሁም“ አለው። 9 ካህኑም፥”በዔላ ሸለቆ የገደልከው የፍልስጥኤማዊው የጎልያድ ሰይፍ በጨርቅ ተጠቅልሎ እዚህ ከኤፉዱ ኋላ አለ። ሌላ የጦር መሣሪያ በዚህ የለምና እርሱን ልትወስደው ብትፈልግ ውሰደው።" ዳዊትም፥ "እንደ እርሱ ያለ ሌላ ሰይፍ የለም፤ እርሱን ስጠኝ" አለው። 10 በዚያን ቀን ዳዊት ተነሥቶ ከሳኦል ፊት ሸሸ፥ ወደ ጌት ንጉሥ ወደ አንኩስም ሄደ። 11 የአንኩስ አገልጋዮችም ንጉሡን፥ "ይህ የምድሪቱ ንጉሥ የሆነው ዳዊት አይደለም? 'ሳኦል ሺዎችን ገደለ፥ ዳዊት ዐሥር ሺዎችን ገደለ' እያሉ ስለ እርሱ በዘፈን እየተቀባበሉ ዘምረውለት አልነበረም? አሉት። 12 ዳዊት ይህንን ቃል በልቡ አኖረው፥ የጌትን ንጉሥ አንኩስንም እጅግ ፈራው። 13 በፊታቸውም አዕምሮውን ለወጠ፥ በያዙት ጊዜም እንደ ዕብድ ሆነ፤ የቅጥሩን በር እየቧጨረም ለሃጩን በጺሙ ላይ አዝረከረከ። 14 አንኩስም አገልጋዮቹን፥ “ተመልከቱ፥ ሰውዬው ዕብድ እንደሆነ ታያላችሁ። 15 ወደ እኔ ለምን አመጣችሁት? ይህንን ሰው በፊቴ እንዲያብድ ወደ እኔ ያመጣችሁት ያበዱ ሰዎችን ስላጣሁኝ ነው? በእርግጥ እንዲህ ያለው ሰው ወደ ቤቴ ይገባል?” አላቸው።



Chapter 22

1 ስለዚህ ዳዊት ያንን ትቶ ወደ ዓዶላም ዋሻ አመለጠ። ወንድሞቹና የአባቱ ቤተሰብ በሙሉ ይህንን በሰሙ ጊዜ ወደዚያ ወደ እርሱ ወረዱ። 2 የተጨነቁ፥ ዕዳ ያለባቸውና የተከፉ ሁሉ ወደ እርሱ ተሰበሰቡ። ዳዊትም አዛዣቸው ሆነ። ከእርሱም ጋር ወደ አራት መቶ የሚጠጉ ሰዎች ነበሩ። 3 ዳዊት ከዚያ በሞዓብ ወዳለችው ወደ ምጽጳ ሄደ። እርሱም የሞዓብን ንጉሥ፥ “እግዚአብሔር የሚያደርግልኝን እስካውቅ ድረስ እባክህን አባቴና እናቴ አንተጋ እንዲኖሩ ፈቃድህ ይሁን” አለው። 4 እነርሱንም በሞዓብ ንጉሥ ዘንድ ተዋቸው። ዳዊት በጠንካራው ምሽግ ውስጥ በነበረበት ጊዜ ሁሉ አባቱና እናቱ ከንጉሡ ጋር ኖሩ። 5 ከዚያም ነቢዩ ጋድ ዳዊትን፥ “በጠንካራው ምሽግ ውስጥ አትቆይ። እርሱን ትተህ ወደ ይሁዳ ምድር ሂድ” አለው። ስለዚህ ዳዊት ያንን ትቶ ወደ ሔሬት ጫካ ሄደ። 6 ዳዊት ከእርሱ ጋር ከነበሩት ሰዎች ጋር መገኘቱን ሳኦል ሰማ። ሳኦል በጊብዓ ከአጣጥ ዛፍ ስር በእጁ ጦሩን እንደያዘ ተቀምጦ ነበር፥ አገልጋዮቹም ሁሉ በዙሪያው ቆመው ነበር። 7 ሳኦል በዙሪያው የቆሙትን አገልጋዮቹን እንዲህ አላቸው፥ “እናንተ የብንያም ሰዎች ሆይ፥ አሁን ስሙ! የእሴይ ልጅ ለእያንዳንዳችሁ እርሻና የወይን ቦታ ይሰጣችኋል? ሁላችሁም በእኔ ላይ ስላደማችሁበት ምትክ ሻለቆችና መቶ አለቆችስ አድርጎ ይሾማችኋል? 8 ልጄ ከእሴይ ልጅ ጋር ቃል ኪዳን ባደረገ ጊዜ ከእናንተ አንዱም አልነገረኝም። አንዳችሁም ስለ እኔ አላዘናችሁም። ልጄ አገልጋዬን ዳዊትን በእኔ ላይ ሲያነሣሣው ከእናንተ ማንም አልነገረኝም። ዛሬ ተደብቋል፥ እኔን ለማጥቃትም ይጠባበቃል።" 9 ከዚያም በሳኦል አገልጋዮች መካከል ቆሞ የነበረው ኤዶማዊው ዶይቅ፥ "የእሴይን ልጅ ወደ ኖብ፥ ወደ አኪጦብ ልጅ ወደ አቢሜሌክ መጥቶ አይቼዋለሁ። 10 አቤሜሌክም እግዚአብሔር ዳዊትን እንዲረዳው ጸለየለት፥ እርሱም ስንቅና የፍልስጥኤማዊውን የጎልያድን ሰይፍ ሰጠው" አለው። 11 ንጉሡም የአኪጦብን ልጅ ካህኑን አቢሜሌክንና የአባቱን ቤተሰብ በሙሉ፥ እንዲሁም በኖብ ይኖሩ የነበሩትን ካህናት እንዲጠራ መልዕክተኛ ላከ። ሁሉም ወደ ንጉሡ መጡ። 12 ሳኦልም፥ "የአኪጦብ ልጅ ሆይ፥ አሁን ስማ!" አለው። እርሱም፥ "ጌታዬ ሆይ፥ ይኸው አለሁ” ብሎ መለሰለት። 13 ሳኦልም እንዲህ አለው፥ “አንተና የእሴይ ልጅ በእኔ ላይ ያሤራችሁት ለምንድነው? ዛሬ እንደሚያደርገው ሁሉ በእኔ ላይ እንዲነሣና በምስጢራዊ ቦታ እንዲደበቅ እንጀራና ሰይፍ ሰጠኸው፥ ይረዳው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር የጸለይክለት ለምንድነው?” 14 አቢሜሌክም ለንጉሡ፥ “የንጉሡ አማችና በጠባቂዎቹ ላይ የበላይ የሆነ፥ በቤትህም የተከበረ፥ በአገልጋዮችህ ሁሉ መካከል እንደ ዳዊት የታመነ ማነው? 15 እግዚአብሔር እንዲረዳው ስጸልይለት የዛሬው የመጀመሪያዬ ነውን? ይህ ከእኔ ይራቅ! ንጉሡ ምንም ነገር በአገልጋይህ ወይም በአባቴ ቤት ሁሉ ላይ አያኑር። አገልጋይህ ከዚህ ሁሉ ነገር አንዱንም አላውቅምና" ብሎ መለሰለት። 16 ንጉሡም፥ "አቢሜሌክ ሆይ፥ አንተና የአባትህ ቤት በሙሉ በእርግጥ ትሞታላችሁ" ብሎ መለሰለት። 17 ንጉሡም በዙሪያው የቆሙትን ጠባቂዎች፥ "መሸሹን እያወቁ አላስታወቁኝምና፥ እጃቸውም ከዳዊት ጋር ነውና፥ ዙሩና የእግዚአብሔርን ካህናት ግደሏቸው” አላቸው። የንጉሡ አገልጋዮች ግን የእግዚአብሔርን ካህናት ለመግደል እጆቻቸውን አላነሡም። 18 ከዚያም ንጉሡ ዶይቅን፥ "ዙርና ካህናቱን ግደላቸው" አለው። ስለዚህ ኤዶማዊው ዶይቅ ዞረና መታቸው፤ በዚያም ቀን ከተልባ እግር የተሠራ ኤፉድ የለበሱ ሰማንያ አምስት ሰዎችን ገደለ። 19 እርሱም የካህናቱን ከተማ ኖብን፥ ወንዶችንና ሴቶችን፥ ልጆችንና ሕፃናትን፥ በሬዎችን፥ አህዮችንና በጎችን በሰይፍ ስለት መታቸው። ሁሉንም በሰይፍ ስለት ገደላቸው። 20 ነገር ግን አብያታር የተባለው የአኪጦብ ልጅ፥ የአቢሜሌክ ልጅ አመለጠ፥ ወደ ዳዊትም ሸሸ። 21 አብያታርም ሳኦል የእግዚአብሔርን ካህናት እንደ ገደለ ለዳዊት ነገረው። 22 ዳዊትም አብያታርን፥ “ኤዶማዊው ዶይቅ በዚያ በነበረ ጊዜ በእርግጥ ለሳኦል እንደሚነግረው በዚያን ቀን ዐውቄ ነበር። ለአባትህ ቤተ ሰብ ሁሉ መሞት ተጠያቂው እኔ ነኝ! ። 23 ከእኔ ጋር ተቀመጥ፥ አትፍራ። ያንተን ነፍስ የሚፈልግ የእኔንም ነፍስ የሚፈልግ ነው። ከእኔ ጋር በሰላም ትኖራለህ” አለው።



Chapter 23

1 ለዳዊትም፥ "ፍልስጥኤማውያን ቅዒላን በመውጋት ላይ ናቸው፥ ዐውድማውንም እየዘረፉ ነው“ ብለው ነገሩት። 2 ስለዚህ ዳዊት እግዚአብሔር እንዲረዳው ጸለየ፥ እርሱም፥”እነዚህን ፍልስጥኤማውያን ሄጄ ልምታቸው? “ ብሎ ጠየቀ። እግዚአብሔርም ዳዊትን፥”ሂድና ፍልስጥኤማውያንን ምታ፥ ቅዒላንም አድን“ አለው። 3 የዳዊት ሰዎችም፥”ተመልከት፥ እዚሁ በይሁዳ ሆነን እየፈራን ነው። በፍልስጥኤማውያን ላይ ወደ ቅዒላ ለመውጣትማ ይልቁን እንዴት አስፈሪ አይሆንብንም? “ አሉት። 4 ከዚያም ዳዊት እግዚአብሔር እንዲረዳው እንደገና ጸለየ። እግዚአብሔርም፥”ተነሥ፥ ወደ ቅዒላ ውረድ። በፍልስጥኤማውያን ላይ ድልን እሰጥሃለሁ“ ብሎ መለሰለት። 5 ዳዊትና ሰዎቹም ሄደው ከፍልስጥኤማውያን ጋር ተዋጉ። የቀንድ ከብቶቻቸውን ወሰዱ፥ እነርሱንም በታላቅ አገዳደል መቷቸው። ስለዚህ ዳዊት የቅዒላን ነዋሪዎች አዳናቸው። 6 የአቢሜሌክ ልጅ አብያታር ወደ ቅዒላ ወደ ዳዊት በሸሸ ጊዜ ኤፉዱን ይዞ ወርዶ ነበር። 7 ዳዊት ወደ ቅዒላ መሄዱ ለሳኦል ተነገረው። ሳኦልም፥ "በሮችና መቀርቀሪያዎች ወዳሏት ከተማ በመግባቱ በራሱ ላይ ዘግቷልና እግዚአብሔር በእጄ ላይ ጥሎታል" አለ። 8 ሳኦልም ወደ ቅዒላ ወርደው ዳዊትንና ሰዎቹን እንዲከቡ ሠራዊቱን ሁሉ ለጦርነት ጠራቸው። 9 ዳዊትም ሳኦል ክፉ ሊያደርግበት እንዳቀደ ዐወቀ። እርሱም ካህኑን አብያታርን፥ "ኤፉዱን ወደዚህ አምጣው" አለው። 10 ዳዊትም፥ "የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፥ ሳኦል በእኔ ምክንያት ከተማይቱን ለማጥፋት ወደ ቅዒላ ለመምጣት እንደሚፈልግ አገልጋይህ በእርግጥ ሰምቷል። 11 አገልጋይህ እንደ ሰማው፥ ሳኦል ወደዚህ ይወርዳል? የቅዒላ ሰዎችስ በእጁ አሳልፈው ይሰጡኝ ይሆን? የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፥ እባክህን ለአገልጋይህ እንድትነግረኝ እለምንሃለሁ” አለ። እግዚአብሔርም፥ “አዎን፥ ወደዚህ ይወርዳል” አለው። 12 ዳዊትም፥ “የቅዒላ ሰዎች እኔንና ሰዎቼን በሳኦል እጅ አሳልፈው ይሰጡናልን?” ብሎ ጠየቀው። እግዚአብሔርም፥ “አሳልፈው ይሰጧችኋል" አለ። 13 ከዚያም ዳዊትና ወደ ስድስት መቶ የሚደርሱ ሰዎቹ ተነሡ፥ ከቅዒላም ወጥተው ሄዱ፥ ከቦታ ቦታም እየተዘዋወሩ ሄዱ። ዳዊት ከቅዒላ መሸሹ ለሳኦል ተነገረው፥ እርሱም ማሳደዱን አቆመ። 14 ዳዊትም በዚፍ ምድረ በዳ ውስጥ ባለው በኮረብታማው አገር፥ በምድረ በዳው ባለ ምሽግ ውስጥ ኖረ። ሳኦል በየቀኑ ይፈልገው ነበር፥ እግዚአብሔር ግን በእጁ ላይ አልጣለውም። 15 ዳዊት በዚፍ ምድረ በዳ ሖሬሽ በተባለ ቦታ ነበር፤ ሳኦልም የእርሱን ሕይወት ለማጥፋት እንደ ወጣ አየ። 16 ከዚያም የሳኦል ልጅ ዮናታን ተነሥቶ በሖሬሽ ወደሚገኘው ወደ ዳዊት ሄደ፥ በእግዚአብሔር ስም አበረታታው። 17 እንዲህም አለው፥ "የአባቴ የሳኦል እጅ አያገኝህምና አትፍራ። አንተ በእስራኤል ላይ ንጉሥ ትሆናለህ፥ እኔም ምክትልህ እሆናለሁ። አባቴ ሳኦልም ደግሞ ይህንን ያውቃል።" 18 እነርሱም በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን አደረጉ። ዳዊት በሖሬሽ ቆየ፥ ዮናታንም ወደ ቤቱ ተመለሰ። 19 ዚፋውያንም በጊብዓ ወዳለው ወደ ሳኦል መጥተው፥ "ዳዊት ከየሴሞን በስተደቡብ በሚገኘው በኤኬላ ኮረብታ ላይ፥ በሖሬሽ ምሽጎች ውስጥ በመካከላችን ተደብቋል፤ 20 አሁንም ንጉሥ ሆይ! ወደዚህ ውረድ፥ ደስ ባለህ ጊዜ ወደዚህ ውረድ! በንጉሡ እጅ አሳልፎ የመስጠቱ ድርሻ የእኛ ይሆናል” አሉት። 21 ሳኦልም፥ “ስለ እኔ ተቆርቁራችኋልና እግዚአብሔር ይባርካችሁ። 22 ሂዱና በይበልጥ እርግጠኛ ሁኑ። የት እንደ ተደበቀና በዚያ ማን እንዳየው መርምሩና ዕወቁ። እጅግ ተንኮለኛ ስለመሆኑ ተነግሮኛል። 23 ስለዚህ ልብ በሉ፥ ራሱን የሚደብቅባቸውን ቦታዎች በሙሉ መርምሩ። የተረጋገጠ መረጃ ይዛችሁልኝ ተመለሱ፥ ከዚያ በኋላ እኔም ከእናንተ ጋር እሄዳለሁ። በምድሪቱ ላይ ካለ፥ በይሁዳ ሺዎች ሁሉ መካከል እፈልገዋለሁ” አላቸው። 24 እነርሱም ተነሡ፥ ሳኦልንም ቀድመው ወደ ዚፍ ሄዱ። ዳዊትና ሰዎቹ ከየሴሞን በስተደቡብ በዓረባ በምትገኘው በማዖን ምድረ በዳ ውስጥ ነበሩ። 25 ሳኦልና ሰዎቹም እርሱን ሊፈልጉት ሄዱ። ይህም ለዳዊት ተነገረው፥ ስለዚህ ወደ ዐለታማው ኮረብታ ወርዶ በማዖን ምድረ በዳ ውስጥ ኖረ። ሳኦል በሰማ ጊዜ ዳዊትን በማዖን ምድረ በዳ አሳደደው። 26 ሳኦል በተራራው በአንዱ ወገን ሄደ፥ ዳዊትና ሰዎቹም በተራራው በወዲያኛው ወገን ይሄዱ ነበር። ዳዊት ከሳኦል ለማምለጥ ተቻኮለ። ሳኦልና ሰዎቹ ዳዊትንና ከእርሱ ጋር የነበሩትን ሰዎች ለመያዝ እየከበቧቸው በነበሩበት ጊዜ 27 አንድ መልዕክተኛ ወደ ሳኦል መጥቶ፥ “ፍልስጥኤማውያን ምድሪቱን ወረዋታልና ፈጥነህ ና" አለው። 28 ስለዚህ ሳኦል ዳዊትን ከማሳደድ ተመልሶ ፍልስጥኤማውያንን ለመዋጋት ሄደ። በዚህ ምክንያት ያ ስፍራ የማምለጫ ዐለት ተብሎ ተጠራ። 29 ዳዊት ከዚያ ወጥቶ በዓይንጋዲ ባሉ ምሽጎች ውስጥ ኖረ።



Chapter 24

1 ሳኦል ፍልስጥኤማውያንን ከማሳደድ በተመለሰ ጊዜ፥ "ዳዊት በዓይንጋዲ ምድረ በዳ ውስጥ ነው" ተብሎ ተነገረው። 2 ከዚያም ሳኦል ከእስራኤል ሁሉ የተመረጡትን ሦስት ሺህ ሰዎች ይዞ ዳዊትንና ሰዎቹን ለመፈለግ ወደ ዓይንጋዲ ሄደ። 3 እርሱም በመንገዱ በበጎች ማደሪያ አቅራቢያ ወደነበረ ዋሻ መጣ። ሳኦልም ለመጸዳዳት ወደዚያ ገባ። ዳዊትና ሰዎቹ በዋሻው ውስጥ ከኋላ ጥጉጋ ተቀምጠው ነበር። 4 የዳዊት ሰዎችም፥ "'ደስ ያሰኘህን እንድታደርግበት ጠላትህን በእጅህ ላይ አሳልፌ እሰጥሃለሁ' ባለህ ጊዜ እግዚአብሔር የተናገረው ስለዚህ ቀን ነው” አሉት። ከዚያም ዳዊት ተነሥቶ በጸጥታ በደረቱ እየተሳበ ወደ ፊት በመሄድ የሳኦልን የካባውን ጫፍ ቆረጠው። 5 ከዚህ በኋላ የሳኦልን የካባውን ጫፍ ስለ ቆረጠ ዳዊትን ኅሊናው ወቀሰው። 6 እርሱም ሰዎቹን፥ "እግዚአብሔር በቀባው በጌታዬ ላይ እጄን በማንሣት እንዲህ ያለውን ነገር ማድረግን እግዚአብሔር ከእኔ ያርቀው" አላቸው። 7 ስለዚህ ዳዊት የእርሱን ሰዎች በዚህ ቃል ገሰጻቸው፥ በሳኦል ላይ አደጋ እንዲጥሉበት አልፈቀደላቸውም። ሳኦል ተነሥቶ ከዋሻው ወጣና መንገዱን ቀጠለ። 8 ከዚህ በኋላ ዳዊት ተነሥቶ ከዋሻው በመውጣት ሳኦልን፥ "ጌታዬ፥ ንጉሥ ሆይ!" በማለት ተጣራ። ሳኦል ወደ ኋላው ዘወር ብሎ በተመለከተ ጊዜ፥ ዳዊት በመስገድ አክብሮትን አሳየው። 9 ዳዊትም ሳኦልን፥ “ 'ዳዊት ሊጎዳህ ይፈልጋል' የሚሉህን ሰዎች ለምን ትሰማቸዋለህ? 10 በዋሻው በነበርን ጊዜ እግዚአብሔር ዛሬ እጄ ላይ ጥሎህ እንደነበረ ዓይኖችህ አይተዋል። አንዳንዶቹ እንድገድልህ ነግረውኝ ነበር፥ እኔ ግን ራራሁልህ። እኔም፥ 'በእግዚአብሔር የተቀባ ስለሆነ፥ በጌታዬ ላይ እጄን አላነሣም' አልኩኝ። 11 አባቴ ሆይ ተመልከት፥ በእጄ ላይ ያለውን የካባህን ቁራጭ ተመልከት። የካባህን ጫፍ ቆረጥኩኝ እንጂ አልገደልኩህም፥ በመሆኑም በእጄ ላይ ክፋትና ክህደት እንደሌለ ዕወቅ፤ ምንም እንኳን ሕይወቴን ለማጥፋት ብታሳድደኝም፥ እኔ አልበደልኩህም። 12 እግዚአብሔር በእኔና በአንተ መካከል ይፍረድ፥ እግዚአብሔር ይበቀልልኝ፥ እጄ ግን ባንተ ላይ አትሆንም። 13 የጥንቱ ምሳሌ፥ 'ከክፉ ሰው ክፋት ይወጣል' ይላል። እጄ ግን ባንተ ላይ አትሆንም። 14 የእስራኤል ንጉሥ የወጣው በማን ላይ ነው? የምታሳድደው ማንን ነው? የሞተን ውሻ! ቁንጫን! 15 እግዚአብሔር ፈራጅ ይሁን፥ በእኔና በአንተ መካከል ይመልከት፥ ይፍረድም፥ ጉዳዬን ተመልክቶም ከእጅህ እንዳመልጥ ይርዳኝ።” 16 ዳዊት ይህንን ቃል ለሳኦል ተናግሮ በጨረሰ ጊዜ፥ ሳኦል፥ “ልጄ ዳዊት! ይህ ድምፅህ ነው?” አለው። ሳኦልም ድምፁን አሰምቶ አለቀሰ። 17 እርሱም ዳዊትን እንዲህ አለው፥ "በክፋት ስመልስልህ በደግነት መልሰህልኛልና ከእኔ ይልቅ አንተ ጻድቅ ነህ። 18 እግዚአብሔር በእጅህ ላይ በጣለኝ ጊዜ አልገደልከኝምና በጎነትን እንዳደረግህልኝ ዛሬ አሳይተሃል። 19 አንድ ሰው ጠላቱን ቢያገኘው በሰላም ያሰናብተዋል? ዛሬ ስላደረግህልኝ ነገር እግዚአብሔር ቸርነትን ያድርግልህ። 20 አሁንም፥ በእርግጥ ንጉሥ እንደምትሆንና የእስራኤል መንግሥት በእጅህ እንደሚጸና ዐውቃለሁ። 21 ከእኔ በኋላ ዘሮቼን እንደማታጠፋና ስሜንም ከአባቴ ቤት እንደማትደመስሰው በእግዚአብሔር ማልልኝ።" 22 ስለዚህ ዳዊት ለሳኦል ማለለት። ከዚያም ሳኦል ወደ ቤቱ ሄደ፥ ዳዊትና ሰዎቹ ግን ወደ አምባው ወጡ።



Chapter 25

1 ሳሙኤል ሞተ። እስራኤላውያን ሁሉ ተሰብስበው አለቀሱለት፥ በራማም በቤቱ ቀበሩት። ከዚያም ዳዊት ተነሥቶ ወደ ፋራን ምድረ በዳ ወረደ። 2 በማዖን አንድ ሰው ነበር፥ ንብረቱም በቀርሜሎስ ይኖር ነበር። ሰውዬው እጅግ ባለጸጋ ነበር። እርሱም ሦስት ሺህ በጎችና አንድ ሺህ ፍየሎች ነበሩት። በቀርሜሎስም በጎቹን ይሸልት ነበር። 3 የሰውየው ስም ናባል፥ የሚስቱም ስም አቢግያ ነበር። ሴቲቱ ብልህና መልኳም የተዋበ ነበረች። ሰውየው ግን አስቸጋሪና በምግባሩ ክፉ ነበር። እርሱም የካሌብ ቤተ ሰብ ተወላጅ ነበር። 4 ዳዊት በምድረ በዳ ውስጥ ሳለ ናባል በጎቹን እንደሚሸልት ሰማ። 5 ስለዚህ ዳዊት ዐሥር ወጣቶችን ላከ። ዳዊትም ወጣቶቹን እንዲህ አላቸው፥ “ወደ ቀርሜሎስ ውጡ፥ ወደ ናባልም ሂዱና በስሜ ሰላምታ አቅርቡለት። 6 እርሱንም እንዲህ በሉት፥ 'በብልጽግና ኑር፥ ሰላም ላንተ፥ ለቤትህና ያንተ ለሆነው ሁሉ ይሁን። 7 ሸላቾች እንዳሉህ ሰምቻለሁ። እረኞችህ ከእኛ ጋር ነበሩ፥ ምንም ጉዳት አላደረስንባቸውም፥ በቀርሜሎስ በነበሩበት ጊዜ ሁሉ አንድም አላጡም። 8 ወጣቶችህን ጠይቃቸው፥ እነርሱም ይነግሩሃል። አሁንም በግብዣህ ቀን መጥተናልና ወጣቶቼ በዓይንህ ፊት ሞገስ ያግኙ። በእጅህ ያለውን ማንኛውንም ነገር ለአገልጋዮችህና ለልጅህ ለዳዊት እባክህን ስጠው።" 9 የዳዊት ወጣቶች በደረሱ ጊዜ፥ በዳዊት ስም ይህንን ሁሉ ለናባል ነገሩትና ምላሹን ጠበቁ። 10 ናባልም ለዳዊት አገልጋዮች፥ "ዳዊት ማነው? የእሴይስ ልጅ ማነው? በእነዚህ ቀናት ከጌቶቻቸው የሚኮበልሉ ብዙ አገልጋዮች አሉ። 11 ታዲያ እንጀራዬን፥ ውሃዬንና ለሸላቾቼ ያረድኩትን ሥጋ ወስጄ ከየት እንደ መጡ ለማላውቃቸው ሰዎች መስጠት ይኖርብኛል?" ሲል መለሰላቸው። 12 ስለዚህ የዳዊት ወጣቶች ዞረው በመመለስ የተባለውን ሁሉ ነገሩት። 13 ዳዊትም ሰዎቹን፥ "ሁሉም ሰው ሰይፉን ይታጠቅ" አለ። ስለዚህ ሁሉም ሰይፎቻቸውን ታጠቁ። ዳዊትም ደግሞ ሰይፉን ታጠቀ። አራት መቶ የሚያህሉ ሰዎች ዳዊትን ተከተሉት፥ ሁለት መቶዎቹም ከስንቅና ትጥቃቸው ጋር ቆዩ። 14 ነገር ግን ከወጣቶቹ አንዱ፥ ለናባል ሚስት ለአቢግያ እንዲህ ሲል ነገራት፥”ዳዊት ከምድረ በዳ ለጌታችን ሰላምታ ለማቅረብ መልዕክተኞች ላከ፥ ጌታችን ግን ሰደባቸው። 15 ሰዎቹ ግን ለእኛ በጣም ጥሩዎች ነበሩ። በመስኩ ላይ እያለን ከእነርሱ ጋር በሄድንበት ጊዜ ሁሉ አንድም አልጎደለብንም፥ እነርሱም አልጎዱንም። 16 በጎቹን እየጠበቅን ከእነርሱ ጋር በቆየንበት ጊዜ ሁሉ ቀንና ሌሊት አጥር ሆነውልን ነበር። 17 በጌታችንና በቤተሰቡ ሁሉ ላይ ክፉ ታስቦአልና ይህንን ዕወቂ፥ ምን ማድረግ እንዳለብሽም አስቢበት። እርሱ የሚረባ ሰው አይደለምና ማንም ሊያነጋግረው አይችልም“። 18 አቢግያም ፈጥና ሁለት መቶ እንጀራ፥ ሁለት ጠርሙስ የወይን ጠጅ፥ ቀደም ብሎ የተዘጋጀ አምስት በግ፥ አምስት መስፈሪያ የተጠበሰ እሸት፥ አንድ መቶ የወይን ዘለላና ሁለት መቶ የበለስ ፍሬ ጥፍጥፍ ወስዳ በአህዮች ላይ ጫነች። 19 ከእርሷ ጋር የነበሩትንም ወጣቶች፥ "በፊቴ ቅደሙ፥ እኔም እከተላችኋለሁ" አለቻቸው። ለባልዋ ለናባል ግን አልነገረችውም። 20 እርሷም በአህያዋ ላይ በመቀመጥ ተራራውን ተከልላ በመውረድ ላይ እያለች ዳዊትና ሰዎቹ ወደ እርሷ ወረዱ፥ እርሷም አገኘቻቸው። 21 ዳዊትም፥”የእርሱ ከሆነው ሁሉ አንድ እንኳን እንዳይጠፋበት፥ ይህ ሰው የነበረውን ሁሉ በምድረ በዳ መጠበቄ በእርግጥም በከንቱ ነበር፥ ስላደረግሁት በጎነት ክፋትን መልሶልኛልና። 22 ነገ ጠዋት የእርሱ ከሆነው ሁሉ አንድ ወንድ እንኳን ባስቀርለት እግዚአብሔር በእኔ በዳዊት ላይ ይህንኑ ያድርግብኝ፥ ደግሞም ይጨምርብኝ" ብሎ ነበር። 23 አቢግያ ዳዊትን ባየችው ጊዜ፥ ከአህያዋ ላይ ፈጥና ወረደች፥ በዳዊትም ፊት አጎንብሳ ወደ ምድር ሰገደች። 24 በእግሩ ላይ ወድቃም እንዲህ አለችው፥ "ጌታዬ ሆይ፥ በደሉ በእኔ ላይ ብቻ ይሁን። እባክህን አገልጋይህ እንድናገርህ ፍቀድልኝ፥ የአገልጋይህንም ቃል ስማ። 25 ጌታዬ ለዚህ ለማይረባው ናባል ትኩረት አይስጥ፥ እርሱ እንደ ስሙ ነው። ስሙ ናባል ነውና ጅልነትም ከእርሱ ጋር ነው። እኔ አገልጋይህ ግን የላካቸውን የጌታዬን ወጣቶች አላየሁም። 26 አሁንም ጌታዬ ሆይ፥ በሕያው እግዚአብሔር ስም፥ በሕያው ነፍስህም እምላለሁ፤ ደም ከማፍሰስና በራስህ እጅ ከመበቀል እግዚአብሔር አግዶሃልና፥ አሁንም ጠላቶችህና በጌታዬ ላይ ክፉ ለማድረግ የሚፈልጉ እንደ ናባል ይሁኑ። 27 አሁንም አገልጋይህ ወደ ጌታዬ ያመጣሁት ይህ ስጦታ ጌታዬን ለሚከተሉ ወጣቶች ይሰጥ። 28 እባክህን የአገልጋይህን መተላለፍ ይቅር በል፥ አንተ ጌታዬ፥ የእግዚአብሔርን ጦርነት በመዋጋት ላይ ስላለህ፥ እግዚአብሔር በርግጥ ለጌታዬ እውነተኛ የሆነን ቤት ይሠራል፥ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ ክፋት አይገኝብህም። 29 ሰዎች ተነሥተው ሕይወትህን ለማጥፋት ቢያሳድዱህም የጌታዬ ሕይወት በአምላክህ በእግዚአብሔር በሕያዋን አንድነት የታሰረች ትሆናለች፤ እርሱም የጠላቶችህን ሕይወት ከወንጭፍ ኪስ እንደሚወረወር፥ በወንጭፍ ይወረውራል። 30 ይህ በሆነ ጊዜ፥ እግዚአብሔር ተስፋ የሰጠህን መልካም ነገር ሁሉ ለጌታዬ በፈጸመ ጊዜ፥ በእስራኤልም ላይ መሪ ባደረገህ ጊዜ፥ 31 ይህ ጉዳይ ሐዘን አይሆንብህም፥ ለጌታዬም የልብ ጸጸት አይሆንም፥ ያለ ምክንያት ደም ያፈሰስክ፥ በራስህም እጅ የተበቀልክ አትሆንም። እግዚአብሔር ለጌታዬ ስኬትን ባመጣልህ ጊዜ አገልጋይህን አስበኝ።" 32 ዳዊትም አቢግያን፥ "ዛሬ እንድታገኚኝ የላከሽ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ቡሩክ ይሁን። 33 ደም በማፍሰስ ከሚሆን በደልና በራሴ እጅ ስለ ራሴ ከመበቀል ጠብቀሽኛልና ጥበብሽ የተባረከ ነው፥ አንቺም የተባረክሽ ነሽ። 34 በእውነት፥ አንቺን ከመጉዳት የጠበቀኝ የእስራኤል አምላክ ሕያው እግዚአብሔርን፥ እኔን ለመገናኘት ፈጥነሽ ባትመጪ ኖሮ፥ ያለምንም ጥርጥር ነገ ጠዋት ለናባል አንድ ወንድ ሕፃን ልጅ አይቀርለትም ነበር“ አላት። 35 ስለዚህ ዳዊት ያመጣችለትን ከእጇ ተቀበላት፤ እርሱም፥ "ወደ ቤትሽ በሰላም ሂጂ፤ ይኸው ቃልሽን ሰማሁ፥ ተቀበልኩሽም" አላት። 36 አቢግያም ተመልሳ ወደ ናባል ሄደች፤ እርሱም የንጉሥ ግብዣን የመሰለ ግብዣ በቤቱ ያደርግ ነበር፤ ናባልም በጣም ሰከሮ፥ ልቡም ደስ ብሎት ነበር። ስለዚህ እስኪነጋ ድረስ ምንም ነገር አልነገረችውም። 37 ከነጋ በኋላ፥ የናባል ስካር በበረደ ጊዜ፥ ሚስቱ እነዚህን ነገሮች ነገረችው፤ ልቡ ቀጥ አለ፥ እርሱም እንደ ድንጋይ ሆነ። 38 ዐሥር ቀን ካለፈ በኋላ እግዚአብሔር ናባልን ስለመታው ሞተ። 39 ናባል መሞቱን ዳዊት በሰማ ጊዜ፥”የመሰደቤን ምክንያት ከናባል እጅ የተቀበለና አገልጋዩን ከክፉ የጠበቀ ጌታ እግዚአብሔር ቡሩክ ይሁን። እርሱም የናባልን ክፉ ሥራ በራሱ ላይ መለሰበት“ አለ። ከዚያም ዳዊት ወደ አቢግያ መልዕክተኛ ልኮ ሚስት አድርጎ ሊወስዳት አናገራት። 40 የዳዊት አገልጋዮች ወደ ቀርሜሎስ፥ ወደ አቢግያ በመጡ ጊዜ፥ "ሚስቱ እንድትሆኚው ልንወስድሽ ዳዊት ወዳንቺ ልኮናል" አሏት። 41 እርሷም ተነሣች፥ በግምባርዋ ወደ ምድር ሰግዳ፥ "ይኸው፥ ሴት አገልጋይህ፥ የጌታዬን አገልጋዮች እግር የማጥብ አገልጋይ ነኝ" አለች። 42 አቢግያም ፈጥና ተነሣች፥ ከተከተሏት ከአምስት ሴት አገልጋዮቿ ጋር በአህያ ተቀመጠች፥ የዳዊትን መልዕክተኞች ተከትላ ሄደች፥ ሚስትም ሆነችው። 43 በተጨማሪም ዳዊት ኢይዝራኤላዊቱን አኪናሆምን ሚስት እንድትሆነው ወሰዳት፥ ሁለቱም ሚስቶቹ ሆኑ። 44 ሳኦል የዳዊት ሚስት የነበረችውን ልጁን ሜልኮልን፥ በጋሊም ለሚኖረው ለሌሳ ልጅ ለፈልጢ ሰጥቶ ነበር።



Chapter 26

1 ዚፋውያን ወደ ሳኦል ወደ ጊብዓ መጥተው፥ “ዳዊት በምድረ በዳው ፊት ለፊት በኤኬላ ኮረብታ ላይ ተደብቋል?” አሉት። 2 ከዚያም ሳኦል ተነሣ፥ ከእስራኤል የተመረጡትን ሦስት ሺህ ሰዎች ይዞ ዳዊትን ለመፈለግ ወደ ዚፍ ምድረ በዳ ወረደ። 3 ሳኦልም በምድረ በዳው ፊት ለፊት ባለው በኤኬላ ኮረብታ ላይ፥ በመንገዱ ዳር ሰፈረ። ዳዊት ግን በምድረ በዳው ቆይቶ ነበር፥ ሳኦል በምድረ በዳው ከበስተኋላው እንደመጣ አየ። 4 ስለዚህ ዳዊት ሰላዮችን ላከና በርግጥም ሳኦል በመምጣት ላይ መሆኑን ዐወቀ። 5 ዳዊት ተነሥቶ ሳኦል ወደ ሰፈረበት ስፍራ ሄደ፤ ሳኦልና የሰራዊቱ አዛዥ የኔር ልጅ አበኔር የተኙበትን ስፍራ አየ፤ ሳኦል በሰፈሩ ውስጥ ተኝቶ ነበር፥ ሕዝቡም በዙሪያው ሰፍሮ ነበር፥ ሁሉም እንቅልፍ ወስዷቸው ነበር። 6 ከዚያም ዳዊት ኬጢያዊውን አቢሜሌክንና የኢዮአብን ወንድም የጽሩያን ልጅ አቢሳን፥ "ወደ ሳኦል ወደ ጦር ሰፈሩ ውስጥ ከእኔ ጋር የሚወርድ ማነው?" አላቸው። አቢሳም፥ "እኔ ከአንተ ጋር እወርዳለሁ" አለው። 7 ስለዚህ ዳዊትና አቢሳ በሌሊት ወደ ሰራዊቱ ሄዱ። ሳኦል በሰፈሩ መካከል ተኝቶ፥ ጦሩም ከራስጌው በምድር ላይ ተተክሎ ነበር። አበኔርና ወታደሮቹ በዙሪያው ተኝተው ነበር። 8 አቢሳም ዳዊትን፥ "እግዚአብሔር ዛሬ ጠላትህን በእጅህ ላይ ጣለው። አሁንም፥ በአንድ ምት ብቻ በጦር ከምድር ጋር እንዳጣብቀው ፍቀድልኝ፥ ሁለተኛ መምታትም አያስፈልገኝም" አለው። 9 ዳዊትም አቢሳን እንዲህ አለው፥ "አትግደለው፤ እግዚአብሔር በቀባው ላይ እጁን ዘርግቶ ከበደል መንጻት የሚችል ማነው? 10 ሕያው እግዚአብሔርን! እግዚአብሔር ራሱ ይገድለዋል፥ ወይም ቀኑ ደርሶ ይሞታል፥ ወይም ወደ ጦርነት ሄዶ ይሞታል። 11 እርሱ በቀባው ላይ እጄን ማንሣትን እግዚአብሔር ከእኔ ያርቀው፤ አሁን ግን፥ በራስጌው ያለውን ጦርና የውሃውን ኮዳ ይዘህ እንድንሄድ እለምንሃለሁ።" 12 ስለዚህ ዳዊት በሳኦል ራስጌ የነበረውን ጦርና የውሃ ኮዳ ወሰደና ሄዱ። ከእግዚአብሔር ከባድ እንቅልፍ ስለወደቀባቸው ሁሉም አንቀላፍተው ነበርና አንድም የነቃ፥ ያየ ወይም ያወቀ አልነበረም። 13 ከዚያም ዳዊት በሌላኛው ወገን ወጣ፥ በተራራው ጫፍ ላይም ርቆ ቆመ፤ በመካከላቸው ሰፊ ርቀት ነበረ። 14 ዳዊትም ወደ ኔር ልጅ ወደ አበኔርና ወደ ሕዝቡ ጮኾ፥ "አበኔር ሆይ፥ አትመልስምን?" አለው። አበኔርም፥ "በንጉሡ ላይ የምትጮኸው አንተ ማነህ?" ብሎ መለሰለት። 15 ዳዊትም አበኔርን፥ "አንተ ጀግና አይደለህም? በእስራኤልስ አንተን የሚመስልህ ማነው? ታዲያ ጌታህን ንጉሡን ያልጠበቅኸው ለምንድነው? አንድ ሰው ጌታህን ንጉሡን ለመግደል መጥቶ ነበርና። 16 ይህ ያደረግኸው ነገር መልካም አይደለም። ሕያው እግዚአብሔርን! ሞት የሚገባህ ነህ፥ ምክንያቱም እግዚአብሔር የቀባውን ጌታህን አልጠበቅኸውም። አሁንም፥ የንጉሡ ጦርና በራስጌው የነበረው የውሃ ኮዳ የት እንዳለ ተመልከት" አለው። 17 ሳኦልም የዳዊት ድምፅ መሆኑን ለየና፥ "ልጄ ዳዊት፥ ይህ ድምፅህ ነው?" አለው። ዳዊትም፥ "ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፥ ድምፄ ነው" አለው። 18 እርሱም እንዲህ አለው፥ "ጌታዬ አገልጋዩን የሚያሳድደው ለምንድነው? ምን አድርጌአለሁ? በእጄስ ያለው ክፋት ምንድነው? 19 አሁንም ጌታዬ ንጉሡ የአገልጋይህን ቃል እንድትሰማ እለምንሃለሁ። በእኔ ላይ ያነሣሣህ እግዚአብሔር ከሆነ መስዋዕትን ይቀበል፤ ሰዎች ከሆኑ ግን በእግዚአብሔር ፊት የተረገሙ ይሁኑ፥ 'ሄደህ ሌሎች አማልክቶችን አምልክ' ብለው የእግዚአብሔርን ርስት አጥብቄ እንዳልይዝ ዛሬ አባረውኛልና። 20 ስለዚህ፥ አንድ ሰው በተራሮች ላይ ቆቅን እንደሚያድን፥ የእስራኤል ንጉሥ ቁንጫን ለመፈለግ መጥቷልና ደሜ ከእግዚአብሔር ፊት ርቆ በምድር ላይ እንዲፈስ አታድርግ።“ 21 ከዚያም ሳኦል፥”ኃጢአትን አድርጌአለሁ። ልጄ ዳዊት፥ ተመለስ፤ ዛሬ ሕይወቴ በዐይንህ ፊት ከብራለችና ከእንግዲህ ወዲህ ክፉ አላደርግብህም። ስንፍናን አድርጌአለሁ፥ እጅግም ተሳስቻለሁ“ አለው። 22 ዳዊትም እንዲህ ሲል መለሰለት፥”ንጉሥ ሆይ ተመልከት! ጦርህ ያለው እዚህ ነው፥ ከወጣቶቹ አንዱ ይምጣና ይውሰድልህ። 23 ዛሬ እግዚአብሔር በእጄ ላይ ጥሎህ እያለ በእርሱ የተቀባውን አልመታሁትምና እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ እንደ ጽድቁና ታማኝነቱ ይክፈለው። 24 ተመልከት፥ ዛሬ ሕይወትህ በዐይኔ ፊት እንደ ከበረች የእኔም ሕይወት በእግዚአብሔር ዐይን አብልጣ የከበረች ትሁን፥ ከመከራዬም ሁሉ ያድነኝ።“ 25 ከዚያም ሳኦል ዳዊትን፥”ልጄ ዳዊት፥ በርግጥ ታላላቅ ነገሮችን እንድታደርግና እንዲከናወንልህ የተባረክህ ሁን“ አለው። ስለዚህ ዳዊት መንገዱን ሄደ፥ ሳኦልም ወደ ስፍራው ተመለሰ።



Chapter 27

1 ዳዊትም፥”አሁንም አንድ ቀን በሳኦል እጅ እሞታለሁ፤ ወደ ፍልስጥኤማውያን ምድር ከመሸሽ የሚሻል አማራጭ የለኝም፤ ያን ጊዜ ሳኦል በእስራኤል ወሰኖች ሁሉ ውስጥ እኔን መፈለጉን ያቆማል፤ በዚህ መንገድ ከእጁ አመልጣለሁ" ብሎ በልቡ አሰበ። 2 ዳዊትም ተነሣ፥ እርሱና ከእርሱ ጋር የነበሩት ስድስት መቶ ሰዎች ወደ ጌት ንጉሥ ወደ አሜህ ልጅ ወደ አንኩስ ተሻገሩ። 3 ዳዊትና ሰዎቹ እያንዳንዱ ከቤተሰቡ ጋር፥ እርሱም ከሁለቱ ሚስቶቹ፥ ከኢይዝራኤላዊቱ ከአኪናሆምና የናባል ሚስት ከነበረችው ከቀርሜሎሳዊቷ ከአቢግያ ጋር በጌት ከአንኩስ ጋር ኖሩ። 4 ዳዊት ወደ ጌት መሸሹን ሳኦል ሰማ፥ ስለዚህ ከዚህ በኋላ አልፈለገውም። 5 ዳዊትም አንኩስን፥ "በዐይንህ ፊት ሞገስ አግኝቼ ከሆነ፥ በዚያ እኖር ዘንድ በአገሪቱ ካሉት ከተሞች በአንዲቱ ስፍራ ይስጡኝ፤ አገልጋይህ በንጉሣዊ ከተማ ከአንተ ጋር ለምን ይኖራል?" አለው። 6 ስለዚህ በዚያን ቀን አንኩስ ጺቅላግን ሰጠው፤ እስከዛሬ ድረስ ጺቅላግ የይሁዳ ነገሥታት የሆነችው ለዚህ ነው። 7 ዳዊት በፍልስጥኤም ምድር የኖረበት ቀን ሲቆጠር አንድ ዓመት ከአራት ወር ሆነው። 8 ዳዊትና ሰዎቹ ጌሹራውያንን፥ ጌርዛውያንን እና አማሌቃውያንን በመውረር የተለያዩ ቦታዎችን አጠቁ፤ እነዚህ ሕዝቦች እስከ ሱርና እስከ ግብፅ ምድር ድረስ ባለው አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ናቸው። እነርሱም ከጥንት ጀምሮ በዚያ ምድር ይኖሩ ነበር። 9 ዳዊትም ምድሪቱን መታ፥ ወንዱንም ሆነ ሴቱን በሕይወት አልተወም፤ በጎችን፥ በሬዎችን፥ አህዮችን፥ ግመሎችን እና ልብሶችን ወሰደ፤ ተመልሶም እንደገና ወደ አንኩስ መጣ። 10 አንኩስ፥ "ዛሬ በማን ላይ ወረራ ፈጸማችሁ?" ብሎ ይጠይቅ ነበር፥ ዳዊትም፥ "በይሁዳ ደቡብ ላይ" ወይም "በደቡብ ይረሕምኤላውያን ላይ" ወይም "በደቡብ ቄናውያን ላይ" ብሎ ይመልስለት ነበር። 11 "ስለዚህ ስለ እኛ፥ 'ዳዊት እንዲህና እንዲህ አደረገ' ለማለት እንዳይችሉ" ብሎ ነበርና ዳዊት ወደ ጌት ይዞ ለመምጣት በማሰብ ወንድ ወይም ሴት በሕይወት አያስቀርም ነበር። በፍልስጥኤም አገር በኖረበት ጊዜ ሁሉ ያደረገው እንደዚህ ነበር። 12 አንኩስም፥ "የራሱ የሆነው የእስራኤል ሕዝብ አምርሮ እንዲጠላው አድርጓል፤ ስለዚህ ለዘላለም አገልጋዬ ይሆናል“ ብሎ ስላሰበ ዳዊትን አመነው።



Chapter 28

1 በዚያም ዘመን ፍልስጥኤማውያን ከእስራኤል ጋር ለመዋጋት ሠራዊታቸውን ሁሉ በአንድ ላይ ሰበሰቡ። አንኩስም ዳዊትን፥ “አንተና ሰዎችህ ያለ ጥርጥር ከእኔ ጋር ወደ ጦርነቱ እንደምትወጡ ዕወቅ” አለው። 2 ዳዊትም አንኩስን፥ “ስለዚህ አገልጋይህ ምን ሊያደርግ እንደሚችል ታያለህ” አለው። አንኩስም ዳዊትን፥ “ስለዚህ እኔም በቋሚነት የግል ጠባቂዬ አደርግሃለሁ" አለው። 3 ሳሙኤል ሞቶ ነበር፤ እስራኤል ሁሉ አልቅሰውለት በከተማው በራማም ቀብረውት ነበር። ሳኦል ከሙታንና ከመናፍስት ጋር የሚነጋገሩትን ከምድሪቱ አጥፍቶ ነበር። 4 ፍልስጥኤማውያን በአንድነት ተሰባስበው በመምጣት ሱነም ላይ ሰፈሩ፤ ሳኦልም እስራኤልን በሙሉ በአንድነት ሰብስቦ ጊልቦዓ ላይ ሰፈረ። 5 ሳኦል የፍልስጥኤማውያንን ሰራዊት ባየ ጊዜ ፈራ፥ ልቡም እጅግ ተንቀጠቀጠ። 6 ይረዳው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር በጸለየ ጊዜም እግዚአብሔር በህልም፥ ወይም በኡሪም፥ ወይም በነቢያት አልመለሰለትም። 7 ከዚያም ሳኦል አገልጋዮቹን፥ "ወደ እርሷ ሄጄ ምክሯን እንድጠይቅ ከሞተ ጋር መነጋገር እችላለሁ የምትል ሴት ካለች ፈልጉልኝ" አላቸው። አገልጋዮቹም፥ "ከሞተ ጋር መነጋገር እችላለሁ የምትል ሴት በዓይንዶር አለች" አሉት። 8 ሳኦል ሌላ ልብስ በመልበስ ራሱን ቀይሮ ከሁለት ሰዎች ጋር ሄደ፤ እነርሱም በሌሊት ወደ ሴቲቱ ሄዱ። እርሱም፥ "የምነግርሽን ሰው አስነሥተሽ ከሞተው ጋር በመነጋገር እንድትጠነቁይልኝ እለምንሻለሁ" አላት። 9 ሴቲቱም፥ "ሳኦል ከሙታንና ከመናፍስት ጋር የሚነጋገሩትን ከምድሪቱ በማጥፋት ያደረገውን ታውቃለህ። ታዲያ እንድሞት ለሕይወቴ ወጥመድ የምታዘጋጀው ለምንድነው?" አለችው። 10 ሳኦልም በእግዚአብሔር ስም ምሎላት፥ "ሕያው እግዚአብሔርን! በዚህ ጉዳይ ምንም ቅጣት አይደርስብሽም” አላት። 11 ሴቲቱም፥ “ማንን ላስነሣልህ?” አለችው። ሳኦልም፥ “ ሳሙኤልን አስነሽልኝ” አላት። 12 ሴቲቱም ሳሙኤልን ባየችው ጊዜ በታላቅ ድምፅ ጮኻ ሳኦልን፥ "አንተ ራስህ ሳኦል ሆንህ ሳለ ለምን አታለልከኝ?" አለችው። 13 ንጉሡም፥ "አትፍሪ፤ ምንድነው ያየሽው?" አላት። ሴቲቱም ሳኦልን፥ "አንድ መንፈስ ከምድር ሲወጣ አያለሁ" አለችው። 14 እርሱም፥ “ምን ይመስላል?” አላት። እርሷም፥ "አንድ ካባ የለበሰ ሽማግሌ እየመጣ ነው" አለችው። ሳኦልም ሳሙኤል እንደሆነ ዐወቀ፥ አክብሮቱን ለማሳየትም በምድር ላይ ሰገደለት። 15 ሳሙኤልም ሳኦልን፥ "እኔን በማስነሣት የምታስቸግረኝ ለምንድነው?" አለው። ሳኦልም፥ "በጣም ተጨንቄአለሁ፥ ፍልስጥኤማውያን ጦርነት ዐውጀውብኛል፥ እግዚአብሔር ትቶኛል፥ በሕልምም ሆነ በነቢያት አይመልስልኝም። ምን ማድረግ እንዳለብኝ እንድታስታውቀኝ ለዚህ ነው የጠራሁህ" ብሎ መለሰለት። 16 ሳሙኤልም እንዲህ አለው፥ "ታዲያ እግዚአብሔር ከተወህና ጠላት ከሆነህ የምትጠይቀኝ ምንድነው? 17 እግዚአብሔር አደርገዋለሁ ብሎ የነገረህን እርሱን ነው ያደረገብህ። እግዚአብሔር መንግሥትን ከእጅህ ቀዶ ለሌላ ሰው፥ ለዳዊት ሰጥቶታል። 18 የእግዚአብሔርን ድምፅ ስላልታዘዝክና ጽኑ ቁጣውን በአማሌቅ ላይ ስላልፈጸምክ ዛሬ ይህንን አድርጎብሃል። 19 በተጨማሪም እግዚአብሔር አንተንና እስራኤልን በፍልስጥኤማውያን እጅ አሳልፎ ይሰጣል። አንተና ልጆችህ ነገ ከእኔ ጋር ትሆናላችሁ። በተጨማሪም እግዚአብሔር የእስራኤልን ሰራዊት በፍልስጥኤማውያን እጅ አሳልፎ ይሰጣል።“ 20 ከዚያም ሳኦል በሳሙኤል ቃል ምክንያት እጅግ ስለፈራ ወዲያውኑ በቁመቱ ሙሉ በምድር ላይ ወደቀ። በዚያ ቀንና ሌሊት ምግብ ስላልበላ ምንም አቅም አልነበረውም። 21 ሴቲቱም ወደ ሳኦል መጥታ እጅግ መጨነቁን አየች፥ እርሷም እንዲህ አለችው፥ "እኔ አገልጋይህ ቃልህን ሰምቻለሁ፤ ሕይወቴን በእጄ ላይ ጥዬ የነገርከኝን ቃል ሰምቻለሁ። 22 አሁንም እንግዲህ አንተም ደግሞ የእኔን የአገልጋይህን ቃል እንድትሰማና ጥቂት ምግብ እንዳቀርብልህ እለምንሃለሁ። መንገድህን ለመሄድ ዐቅም እንድታገኝ ብላ። 23 ሳኦል ግን፥ "አልበላም" በማለት እንቢ አለ። ነገር ግን አገልጋዮቹ ከሴቲቱ ጋር በመሆን ለመኑት፥ እርሱም ቃላቸውን ሰማ። ስለዚህ ከምድር ላይ ተነሥቶ ዐልጋ ላይ ተቀመጠ። 24 ሴቲቱም በቤቷ የደለበ ጥጃ ነበራት፤ ፈጥና አረደችው፤ ዱቄትም ወስዳ ለወሰችው፤ ቂጣ አድርጋም ጋገረችው። 25 እርሷም በሳኦልና በአገልጋዮቹ ፊት አቀረበችላቸው፥ እነርሱም በሉ። ከዚያም በዚያው ሌሊት ተነሥተው ሄዱ።



Chapter 29

1 ፍልስጥኤማውያንም ሰራዊታቸውን ሁሉ አፌቅ ላይ ሰበሰቡ፤ እስራኤላውያንም በኢይዝራኤል ምንጭ አጠገብ ሰፈሩ። 2 የፍልስጥኤማውያኑ መሳፍንት በመቶዎችና በሺዎች እየሆኑ አለፉ፤ ዳዊትና ሰዎቹም ከአንኩስ ጋር በደጀንነት አለፉ። 3 ከዚያም የፍልስጥኤም መሳፍንት፥ "እነዚህ ዕብራውያን እዚህ ምን ይሠራሉ?" አሉ። አንኩስም ለሌሎቹ የፍልስጥኤም መሳፍንት፥ "ይህ በእነዚህ ቀናት ሁሉ ከእኔ ጋር የነበረው፥ የእስራኤል ንጉሥ የሳኦል አገልጋይ ዳዊት አይደለምን? ደግሞም በእነዚህ ዓመታት ሁሉ ወደ እኔ ከመጣበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ምንም ስህተት አላገኘሁበትም” አላቸው። 4 ነገር ግን የፍልስጥኤም መሳፍንት በእርሱ ላይ ተቆጥተው፥ “ያንን ሰው ወደ ሰጠኸው ወደ ስፍራው እንዲመለስ አሰናብተው፥ በውጊያው ውስጥ ጠላት እንዳይሆንብን ከእኛ ጋር ወደ ጦርነት አትላከው። ይህ ሰው ከጌታው ጋር ሰላምን የሚፈጥረው በምንድነው? የሰዎቻችንን አንገት በመቁረጥ አይደለምን? 5 ይህ በዘፈን እየተቀባበሉ፥ 'ሳኦል ሺዎችን ገደለ፥ ዳዊት ዐሥር ሺዎችን ገደለ" ያሉለት ዳዊት አይደለምን?" አሉት። 6 ከዚያም አንኩስ ዳዊትን ጠርቶ፥ "ሕያው እግዚአብሔርን! አንተ ጥሩ ሰው ነህ፥ በእኔ አመለካከት በሰራዊቱ ውስጥ መውጣትህና መግባትህ መልካም ነው፤ ወደ እኔ ከመጣህበት ጊዜ ጀምሮ እስከዛሬው ቀን ድረስ ምንም ስህተት አላገኘሁብህም። ይሁን እንጂ መሳፍንቱ አልደገፉህም። 7 ስለዚህ አሁን የፍልስጥኤም መሳፍንት ቅር እንዳይሰኙ ተመለስና በሰላም ሂድ" አለው። 8 ዳዊትም አንኩስን፥ “ግን ምን አድርጌአለሁ፥ እንዳልሄድና ከጌታዬ ከንጉሡ ጠላቶች ጋር እንዳልዋጋ በእነዚህ በፊትህ በኖርኩባቸው ቀናት በአገልጋይህ ላይ ምን አግኝተህብኛል?” አለው። 9 አንኩስም ለዳዊት፥ “አንተ በእኔ ዕይታ ነቀፌታ እንደማይገኝበት እንደ እግዚአብሔር መልአክ ነህ፤ ይሁንና የፍልስጥኤም መሳፍንት፥ 'ከእኛ ጋር ወደ ጦርነት አይሄድም' ብለዋል። 10 ስለዚህ ከአንተ ጋር ከመጡት ከጌታህ አገልጋዮች ጋር ማልዳችሁ ተነሡ፤ ማልዳችሁ ተነሡና ሲነጋላችሁ ሂዱ" ብሎ መለሰለት። 11 ስለዚህ ዳዊትና ሰዎቹ በጠዋት ለመሄድ፥ ወደ ፍልስጥኤማውያንም ምድር ለመመለስ ማልደው ተነሡ። ፍልስጥኤማውያን ግን ወደ ኢይዝራኤል ወጡ።



Chapter 30

1 እንዲህም ሆነ፥ ዳዊትና ሰዎቹ በሦስተኛው ቀን ወደ ጺቅላግ በመጡ ጊዜ አማሌቃውያን በኔጌቭና በጺቅላግ ላይ ወረራ ፈጽመው ነበር። እነርሱም ጺቅላግን መቱ፥ አቃጠሏትም፥ 2 ሴቶችንና በውስጧ የነበረውን ትንሽና ትልቅ ሁሉ ማረኩ። ይዘዋቸው መንገዳቸውን ሄዱ እንጂ አንዱንም አልገደሉም። 3 ዳዊትና ሰዎቹ ወደ ከተማይቱ በመጡ ጊዜ ከተማይቱ በእሳት ተቃጥላ፥ ሚስቶቻቸው፥ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸው ተማርከው ተወስደው ነበር። 4 ከዚያም ዳዊትና ከእርሱ ጋር የነበሩት ሰዎች ለማልቀስ ኃይል እስከማይኖራቸው ድረስ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ። 5 ሁለቱ የዳዊት ሚስቶች፥ ኢይዝራኤላዊቱ አኪናሆምና የቀርሜሎሳዊው የናባል ሚስት የነበረችው አቢግያ ተማርከው ነበር። 6 የሕዝቡም ሁሉ መንፈስ፥ እያንዳንዱም ስለ ወንዶችና ሴቶች ልጆቹ ስላዘነ በድንጋይ ሊወግሩት ይነጋገሩ ስለነበር ዳዊት እጅግ ተጨነቀ፤ ዳዊት ግን በአምላኩ በእግዚአብሔር ራሱን አበረታ። 7 ዳዊትም የአቢሜሌክን ልጅ ካህኑን አብያታርን፥ "ኤፉዱን ወደዚህ እንድታመጣልኝ እለምንሃለሁ" አለው። አብያታር ኤፉዱን ለዳዊት አመጣለት። 8 ዳዊትም ምሪት ለማግኘት ወደ እግዚአብሔር፥ "ይህንን ወራሪ ብከተል እደርስበታለሁ?" ብሎ ጸለየ። እግዚአብሔርም፥ "ተከተላቸው፥ ያለጥርጥር ትደርስባቸዋለህ፥ ሁሉንም ነገር ታስመልሳለህ" ብሎ መለሰለት። 9 ስለዚህ ዳዊትና ከእርሱ ጋር የነበሩት ስድስት መቶ ሰዎች ሄዱ፤ ከእነርሱ ወደ ኋላ የቀሩት ወደሚቆዩበት ወደ ባሦር ወንዝ መጡ። 10 ነገር ግን ዳዊት ከአራት መቶ ሰዎች ጋር መከታተሉን ቀጠለ፤ ሁለት መቶዎቹ በጣም ስለ ደከሙ የባሦርን ወንዝ መሻገር አልቻሉምና ወደ ኋላ ቀሩ። 11 እነርሱም በሜዳው ላይ አንድ ግብፃዊ አገኙና ወደ ዳዊት አመጡት፤ ምግብ ሰጡትና በላ፥ እንዲጠጣም ውሃ ሰጡት፤ 12 ደግሞም ከበለስ ጥፍጥፍ ቁራጭና ሁለት የወይን ዘለላ ሰጡት። ለሦስት ቀንና ሌሊት ምንም ምግብ አልበላም፥ ውሃም አልጠጣም ነበርና በበላ ጊዜ እንደገና ብርታት አገኘ። 13 ዳዊትም፥ "አንተ የማን ነህ? ከየትስ ነው የመጣኸው?" አለው። እርሱም፥ "እኔ የአማሌቃዊ አገልጋይ፥ ግብፃዊ ወጣት ነኝ፤ ከሦስት ቀናት በፊት ታምሜ ስለነበር ጌታዬ ትቶኝ ሄደ። 14 እኛም በከሊታውያን ኔጌቭ፥ የይሁዳ በሆነው ምድርና በካሌብ ኔጌቭ ላይ ወረራ ፈጸምን፥ ጺቅላግንም አቃጠልናት“ አለው። 15 ዳዊትም፥”ወደዚህ ወራሪ አካል መርተህ ልታወርደኝ ትፈቅዳለህ? “ አለው። ግብፃዊውም፥”እንዳትገድለኝ ወይም በጌታዬ እጅ ላይ አሳልፈህ እንዳትሰጠኝ በእግዚአብሔር ማልልኝ እንጂ ወደ ወራሪው አካል መርቼ አወርድሃለሁ“ አለው። 16 ግብፃዊው ዳዊትን እየመራው ወደ ታች ባወረደው ጊዜ፥ ወራሪዎቹ ከፍልስጥኤማውያን ምድርና ከይሁዳ ምድር ከወሰዱት ምርኮ ሁሉ የተነሣ እየበሉና እየጠጡ፥ እየጨፈሩም በምድሩ ሁሉ ተበትነው ነበር። 17 ዳዊትም ደንገዝገዝ ሲል ጀምሮ እስከ ማግስቱ ምሽት ድረስ መታቸው። በግመሎች ተቀምጠው ከሸሹት ከአራት መቶ ወጣቶች በስተቀር አንድም ሰው አላመለጠም። 18 ዳዊት አማሌቃውያን ወስደዋቸው የነበሩትን ሁሉ አስመለሰ፤ ሁለቱን ሚስቶቹንም አዳነ። 19 ትንሽ ይሁን ትልቅ፥ ወንዶች ልጆች ይሁኑ ሴቶች ልጆች፥ ምርኮም ይሁን ወራሪዎቹ ለራሳቸው ከወሰዱት ማንኛውም ነገር አንዱም አልጠፋም። ዳዊት ሁሉን ነገር አስመለሰ። 20 ዳዊትም ሰዎቹ ከሌሎች ከብቶች ፊት ይነዷቸው የነበሩትን የበጉን፥ የፍየሉንና የላሙን መንጋ ሁሉ ወሰደ። እነርሱም፥ "ይህ የዳዊት ምርኮ ነው" አሉ። 21 ዳዊት ሊከተሉት እጅግ ደክሟቸው በባሦር ወንዝ አጠገብ እንዲቆዩ ወደተደረጉት ወደ ሁለት መቶዎቹ ሰዎች መጣ። እነዚህ ሰዎች ዳዊትንና ከእርሱ ጋር የነበሩትን ሰዎች ለመገናኘት ወጡ። ዳዊት ወደ እነዚህ ሰዎች በመጣ ጊዜ ሰላምታ ሰጣቸው። 22 ከዚያም ከዳዊት ጋር ሄደው በነበሩት ሰዎች መካከል ክፉዎችና የማይረቡት ሁሉ፥”እያንዳንዱ ሚስቱንና ልጆቹን ይዞ ከመሄድ በስተቀር እነዚህ ሰዎች ከእኛ ጋር ስላልሄዱ፥ ካስመለስነው ምርኮ ምንም አንሰጣቸውም“ አሉ። 23 ከዚያም ዳዊት፥”ወንድሞቼ ሆይ፥ እግዚአብሔር በሰጠን ነገር እንዲህ ልታደርጉ አይገባም። እርሱ ጠበቀን፥ በእኛ ላይ የመጡትንም ወራሪዎች በእጃችን ላይ አሳልፎ ሰጠን። 24 በዚህ ጉዳይ ማን ይሰማችኋል? ወደ ጦርነት የሄደው የየትኛውም ሰው ድርሻ ስንቅና ትጥቅ ከጠበቀ ከየትኛውም ሰው ድርሻ ጋር እኩል ይሆናል፤ ሁሉም እኩል ይካፈላሉ" አላቸው። 25 ዳዊት ለእስራኤል ደንብና ሥርዓት ስላደረገው፥ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስከዚህ ቀን ድረስ እንደዚሁ ሆነ። 26 ዳዊት ወደ ጺቅላግ በመጣ ጊዜ፥ ከምርኮው ጥቂቱን፥ "ይህ ከእግዚአብሔር ጠላቶች ካገኘነው ምርኮ ለእናንተ የተላከ ስጦታ ነው“ብሎ ለይሁዳ ሽማግሌዎችና ለወዳጆቹ ላከላቸው። 27 የላከውም፥ በቤቴል፥ በደቡብ ራሞት፥ በየቲር፥ 28 በአሮኤር፥ በሢፍሞት፥ በኤሽትሞዓ ለነበሩ ሽማግሌዎች ነበር። 29 እንዲሁም በራካል፥ በይረሕምኤላውያንና በቄናውያን ከተሞች፥ 30 በሔርማ፥ በቦራሣን፥ በዓታክ፥ 31 በኬብሮን፥ እንዲሁም ዳዊት ራሱና ሰዎቹ አዘውትረው ይሄዱባቸው በነበሩ ስፍራዎች ሁሉ ለሚኖሩ ሽማግሌዎች ላከላቸው።



Chapter 31

1 ፍልስጥኤማውያን ከእስራኤል ጋር ተዋጉ። የእስራኤል ሰዎች ከፍልስጥኤማውያን ፊት ሸሹ፥ በጊልቦዓ ተራራ ላይም ተገድለው ወደቁ። 2 ፍልስጥኤማውያንም ሳኦልንና ልጆቹን በቅርብ ርቀት ተከተሏቸው። ፍልስጥኤማውያንም ልጆቹን ዮናታንን፥ አሚናዳብንና ሜልኪሳን ገደሏቸው። 3 ውጊያው በሳኦል ላይ በረታበት፥ ቀስተኞችም አገኙት። በእነርሱም ምክንያት በጽኑ ሕመም ላይ ነበር። 4 ሳኦልም ጋሻ ጃግሬውን፥”ሰይፍህን ምዘዝና ውጋኝ። አለበለዚያ፥ እነዚህ ያልተገረዙ መጥተው ይሳለቁብኛል“ አለው። 5 ጋሻ ጃግሬው ግን እጅግ ፈርቶ ስለነበረ እምቢ እለ። ስለዚህ ሳኦል የራሱን ሰይፍ ወስዶ በላዩ ላይ ወደቀበት። ጋሻ ጃግሬው ሳኦል መሞቱን ባየ ጊዜ እርሱም ደግሞ ሰይፉ ላይ ወድቆ አብሮት ሞተ። 6 ስለዚህ ሳኦል፥ ሦስቱ ወንዶች ልጆቹና ጋሻ ጃግሬው ሞቱ፤ እነዚህ ሰዎች ሁሉ በአንድ ቀን ሞቱ። 7 ከሸለቆው በወዲያኛው ወገን የነበሩትና ከዮርዳኖስ በላይ የነበሩት የእስራኤል ሰዎች፥ የእስራኤል ሰዎች መሸሻቸውን፥ ሳኦልና ልጆቹ መሞታቸውን ባዩ ጊዜ ከተሞቻቸውን ትተው ሸሹ፥ ፍልስጥኤማውያንም መጥተው ተቀመጡባቸው። 8 በማግስቱ እንዲህ ሆነ፥ ፍልስጥኤማውያን የሞቱትን ሰዎች ትጥቅ ለመግፈፍ በመጡ ጊዜ ሳኦልና ሦስቱ ልጆቹ በጊልቦዓ ተራራ ላይ ወድቀው አገኟቸው። 9 እነርሱም ራሱን ቆረጡት፥ የጦር መሣሪያውንም ገፈፉት፥ ወደ ፍልስጥኤማውያን ምድር ሁሉ ለጣዖት መቅደሶቻቸውና ለሕዝቡ ወሬውን እንዲያደርሱ መልዕክተኞችን ላኩ። 10 የጦር መሣሪያውን በአስታሮት መቅደስ ውስጥ አስቀመጡት፥ ሬሳውንም በቤትሳን ከተማ የግንብ አጥር ላይ አንጠለጠሉት። 11 የኢያቢስ ገለዓድ ሰዎች ፍልስጥኤማውያን በሳኦል ላይ ያደረጉትን በሰሙ ጊዜ 12 ተዋጊ የሆኑ ሰዎች ሁሉ ተነሥተው ሌሊቱን ሁሉ ተጉዘው የሳኦልንና የልጆቹን ሬሳ ከአጥሩ ላይ ወሰዱ። ወደ ኢያቢስ ሄዱ፥ በዚያም አቃጠሏቸው። 13 ከዚያም አጥንቶቻቸውን በመውሰድ በኢያቢስ ባለው የአጣጥ ዛፍ ሥር ቀበሯቸው፥ ሰባት ቀንም ጾሙ።



Book: 2 Samuel


2 Samuel

Chapter 1

1 ሳዖል ከሞተ በኋላ፣ ዳዊት በአማሌቃውያን ላይ ጥቃት ከማድረስ በመመለስ በጺቅላግ ሁለት ቀን ቆየ፡፡ 2 በሦስተኛው ቀን የተቀዳደደ ልብስ የለበሰ፣ በራሱም ላይ ትቢያ የነሰነሰ አንድ ሰው ከሳኦል ሰፈር መጣ፡፡ ወደ ዳዊት እንደ ደረሰም ወደ መሬት ለጥ ብሎ ሰገደለት፡፡ 3 ዳዊትም “ከወዴት መጣህ?” ሲል ጠየቀው፡፡ እርሱም፣ “ከእስራኤላውያን ሰፈር አምልጬ የመጣሁ ነኝ” ሲል መለሰ፡፡ 4 ዳዊትም፣ “እስቲ የሆነውን ሁሉ ንገረኝ” አለው፡፡ እርሱም “ሰዎቹ ከጦርነት ሸሽተዋል፤ ብዙዎቹ ወድቀዋል ደግሞም ሞተዋል፤ ሳዖልና ልጁ ዮናታንም ሞተዋል” አለ፡፡ 5 ዳዊትም ለወጣቱ፤ “ሳኦልና ልጁ ዮናታን መሞታቸውን እንዴት አወቅህ?” ሲል ጠየቀው፡፡ 6 ወጣቱም እንዲህ ሲል መለሰ፤ “ድንገት ወደ ጊልቦዓ ተራራ ወጥቼ ነበር፤ እዚያም ሳኦል ጦሩን ተደግፎ ሳለ፣ ሠረገሎችና ፈረሰኞች ተከታትለው ደረሱበት፤ 7 ወደ ኋላውም ዞር ሲል እኔን ስላየ ጠራኝ፤ እኔም ‘እነሆኝ አለሁ’ አልኩት፡፡ 8 እርሱም፣ ‘አንተ ማን ነህ?’ ሲል ጠየቀኝ፡፡ አኔም፣ ‘አማሌቃዊ ነኝ’ ብዬ መለስሁለት፡፡ 9 እርሱም አለኝ ‘እኔ በታላቅ ስቃይ ውስጥ እገኛለሁ፤ ነፍሴ ግን አልወጣችም፤ እባክህ በላዬ ቆመህ ግደለኝ’ አለኝ፡፡ 10 ስለሆነም፣ ከወደቀ በኋላ እንደማይተርፍ ስላወቅሁ፤ በላዩ ቆሜ ገደልሁት፤ በራሱ ላይ የነበረውን ዘውድና የክንዱን አንባር ወስጄ እነሆ፣ ለጌታዬ አምጥቻለሁ፡፡” አለው፡፡ 11 ከዚያም ዳዊት ልብሱን ቀደደ፤ ከእርሱም ጋር የነበሩት ሁሉ እንደዚሁ አደረጉ፡፡ 12 የወደቁት በሰይፍ ነበርና ለሳኦል ለልጁ ለዮናታንና ለእግዚአብሔር ሕዝብ አዘኑ፤ አለቀሱ፤ እስከ ማታም ድረስ ጾ፡፡ 13 ዳዊትም ወጣቱን ሰውዬ፣ “የየት አገር ሰው ነህ?” ሲል ጠየቀው፡፡ እርሱም፣ “በአገሪቱ ውስጥ በመጻተኛነት የሚኖር አማሌቃዊ ልጅ ነኝ” ብሎ መለሰ፡፡ 14 ዳዊትም፣ “እግዚአብሔር የቀባውን ንጉሥ በገዛ እጅህ ስትገድል ለምን አልፈራህም?” ሲል ጠየቀው፡፡ 15 ዳዊትም ከጎልማሶቹ አንዱን ጠርቶ፣ “ግደለው” አለው፤ ጎልማሳው ሰው ሄዶ መታው፣ አማሌቃዊውም ሞተ፡፡ 16 ከዚያም ዳዊት ለሞተው አማሌቃዊ፣ “‘እግዚአብሔር የቀባውን ገድያለሁ’ ስትል አፍህ መስክሮብሃልና ደምህ በራስህ ላይ ነው” አለው፡፡ 17 ከዚያም ዳዊት ለሳዖልና ለልጁ ለዮናታን የሚከተለውን የሐዘን እንጉርጉሮ አንጎራጎረ፡፡ 18 እንዲሁም የቀስት እንጉርጉሮ የተባለውን ለይሁዳ ሕዝብ እንዲያስተምሩ አዘዘ፤ ይህም በያሸር መጽሐፍ ተጽፎአል፡፡ 19 “እስራኤል ሆይ፣ ክብርህ ሞቶአል፣ በተራሮችህ ላይ ተገድሎአል! ኃያላኑ እንዴት ወደቁ! 20 የፍልስጥኤም ሴቶች ልጆች እንዳይደሰቱ፣ ያልተገረዙት ሴት ልጆች ፌሽታ እንዳያደርጉ ይህን በጌት አትናገሩ፣ በአስቆሎናም መንገዶች አታውጁት፡፡ 21 እናንት የጊልቦዓ ተራሮች ሆይ ጠል አያረስርሳችሁ፣ ዝናብም አይውረድባችሁ፤ የቁርባን እህል የሚያበቅሉም እርሻዎች በዚያ አይኑሩ፤ በዚያ የኃያሉ ሰው ጋሻ ረክሶአልና፣ የሳዖል ጋሻ ከእንግዲህ በዘይት አይወለወልም፡፡ 22 ከሞቱት ሰዎች ደም፣ ከኃያላኑም ገላ የዮናታን ቀስት ተመልሶ አልመጣም፤ የሳዖልም ሰይፍ በከንቱ አልተመለሰም፡፡ 23 ሳዖልና ዮናታን በሕይወት እያሉ የሚዋደዱና ግርማ ያላቸው ነበሩ፤ ሲሞቱም አልተለያዩም፤ከንስርም ይልቅ ፈጣኖች ከአንበሳም ይልቅ ብርቱዎች ነበሩ፡፡ 24 እናንተ የእስራኤል ቆነጃጅት ሆይ፤ ሐምራዊ ቀሚስና ቀጭን ፈትል ላለበሳችሁ ፤ ልብሶቻችሁንም በወርቀ-ዘቦ ላስጌጠላችሁ ለሳዖል አልቅሱለት፡፡ 25 ኃያላን እንዴት እንዲህ በጦርነት መካከል ወደቁ! ዮናታን ከፍ ባሉ ስፍራዎቻችሁ ላይ ሞቶአል፡፡ 26 ወንድሜ ዮናታን ሆይ፤ እኔ ስለ አንተ አዘንሁ፤ አንተ ለእኔ እጅግ ውድ ነበርህ፤ ፍቅርህ ለእኔ ድንቅ ነበር፤ ከሴት ፍቅርም የላቀ ነበር፡፡ 27 ኃያላን እንዴት ወደቁ፤ የጦር መሣሪዎቹስ እንዴት ከንቱ ሆኑ!”



2 Samuel 1:1

ጺቅላግ

ይህ በይሁዳ ደቡባዊ ክፍል የሚገኝ የከተማ ስም ነው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

በሶስተኛው ቀን

"ከሶስት ቀናት በኋላ" (ተከታታይ ቁጥሮች የሚለውን ይመልከቱ)

ልብሱ ተቀዶ እና በራሱ ላይ ትቢያ ነስንሶ

በዚህ ባህል፣ የራስን ልብስ መቅደድ እና በራስ ላይ አመድ መነስነስ የሃዘን መግለጫ ድርጊት ነበር፡፡ (ትዕምርታዊ/ምልክታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

ወደ ምድር ዝቅ ብሎ እና ራሱን ደፍቶ

ይህ አሁን የእስራኤል ንጉሥ ለሆነው ለዳዊት ራሱን ዝቅ አድርጎ ያሳየበት መንገድ ነበር፡፡ (ትዕምርታዊ/ምልክታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

2 Samuel 1:3

ብዙዎች ወደቁ ደግሞም ብዙዎች ሞቱ

ሊሰጡ የሚችሉ ትርጉሞች 1) "ብዙዎች ቆስለው ነበር ደግሞም ብዙዎች ተገድለው ነበር" ወይም 2) "ብዙዎች ቆስለው እና ተገድለው ነበር"

2 Samuel 1:6

በአጋጣሚ በዚያ ተገኝቼ ነበር

ይህ ሃሳብ ትኩረት የሚያደርገው ሰውየው ሳኦልን ለማገኘት እቅድ እንዳነበረው ነው

ሳኦል በጦሩ ላይ ዘመም ብሎ ነበር

ሊሰጡ የሚችሉ ትርጉሞች 1) "ሳኦል ደክሞና ጦሩን ራሱን ለመደገፊያነት ተጠቅሞበት ነበር ወይም 2) ሳኦል በራሱ ጦር ላይ በመውደቅ ራሱን ለመግደል እየሞከረ ነበር፡፡ (ዩፊሚዝም/ የማያስደስትን ቃል ሻል ባለ ቃል መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

2 Samuel 1:8

‘ማን ነህ?' አለኝ፡፡ እኔም እንዲህ ብዬ መለስኩለት፣ ‘እኔ አማሌቃዊ ነኝ፡፡'

ይህ ቀጥተኛ ጥቅስ በርቱዕ/ቀጥተኛ ንግግር ሊገለጽ ይችላል፡፡ "ማን እንደሆንኩ ጠየቀኝ፣ እኔም አማሌቃዊ እንደሆንኩ ነገርኩት" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቀጥተኛ እና ቀጥተኛ ያልሆነ ጥቅሶች የሚለውን ይመልከቱ)

እኔ አማሌቃዊ ነኝ

እነዚህ ህዝቦች ዳዊት በ2 ሳሙኤል 1፡1 ላይ ድል ያደረጋቸው እነዚያው ሰዎች ናቸው፡፡

ታላቅ መከራ አገኘኝ

የሳኦል መከራ የተገለጸው አንዳች አስጨናቂ ነገር አንቆ እንደያዘው ተደርጎ ነው፡፡ "እጅግ ተጨነቅኩ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሰውኛ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

ህይወቴ ገና አላለፈችም/ነፍሴ አልወጣችም

ይህ ፈሊጥ ትረጉሙ እርሱ ገና በህይወት አለ ማለት ነው፡፡ "እስከ አሁን በህይወት አለሁ" (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልከቱ)

ከወደቀ በኋላ በህይወት አይቀጥልም

"መሞቱ አይቀርም"

2 Samuel 1:11

ዳዊት ልብሱን ቀደደ… ከእርሱ ጋር ያሉ ሰዎችም እንደዚያው አደረጉ

ዳዊትና የእርሱ ሰዎች በንጉሥ ሳኦል ሞት ማዘናቸውን ለመግለጽ ልብሳቸውን ቀደዱ፡፡ (ትዕምርታዊ/ምልክታዊ ድርጊት የሚለውን ይመልከቱ)

ለያህዌ ህዝብ፣ እና ለእስራኤል ቤት

ሁለቱ ሃሳቦች በመሰረቱ ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፡፡ "ቤት" የሚለው ቃል የእስራኤልን ትውልዶች የሚወክል ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት/ ነው፡፡ ነገር ግን፣ "ህዝብ" እና "ቤት" የሚሉት ሁለቱም ቃላት ምናልባት የእስራኤልን ወታደሮች የሚወክሉ ስኔክቲክ/የነገሩን ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ/ ናቸው፡፡ "ለእስራኤላውያን ወታደሮች" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ እና ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት እንዲሁም ስኔክቲክ/ የአንድን ነገር ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚሉትን ይመልከቱ)

ያህዌ

ይህ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ራሱን ለህዝቡ የገለጸበት ስም ነው፡፡ ይህ እንዴት እንደሚተረጎም የትርጉም ስለ ያህዌ የቃል ትርጉም ገጽን ይመልከቱ)

በሰይፍ ወደቁ

እዚህ ስፍራ "ወደቁ" የሚለው መገደልን በትሁት መንገድ የሚገልጽ ነው፡፡እንደዚሁም፣ "ሰይፍ" ውጊያን ይወክላል/ይገልጻል፡፡ ይህ በዚህ ስፍራ "ተገድለዋል" ማለት ነው፡፡ "በጦርነት ሞተዋል" ወይም "ጠላቶች በጦርነቱ ገድለዋቸዋል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ዩፊሚዝም/ የማያስደስትን ቃል ሻል ባለ ቃል መተካት እና ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት የሚሉትን ይመልከቱ)

አንተ ከየት ነህ?

በ2ሳሙኤል 1፡8 ውስጥ ሰውየው አስቀድሞውኑ አማሌቃዊ መሆኑን ገልጽዋል፡፡ ዳዊት ሰውየው ይህንን በግልጽ እንዲያረጋግጥለት ይጠይቀዋል፣ ምክንያቱ ዳዊት በሰውየው ላይ ጽኑ ፍርድ ሊፈርድበት ስለሆነ ነው፡፡

2 Samuel 1:14

በእጅህ… ያህዌ የቀባውን ስትገድል ስለ ምን አልፈራህም?

ይህ ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ ያገለገለው ሰውየውን ለመገሰጽ ነው፡፡ ይህ በዐረፍተ ነገር ሊገለጽ ይችላል፡፡ "እጅህ… እርሱ የቀባውን ሲገድል ያህዌን መፍራት ነበረብህ!" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ቃለ ምልልሳዊ ጥያቄ የሚለውን ይመልከቱ)

ያህዌ የቀባው ንጉሥ

ይህ የሚያመለክተው ሳኦልን ነው፡፡

በገዛ እጆችህ

ይህ ሀረግ የሚገልጸው ራስህ አንድ ነገር ማድረግህን ነው፡፡ "ራስህ" ወይም "በግል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

መትተህ ጣለው/ውደቅበት

የዚህ ፈሊጣዊ አነጋገር ትርጉም "ግደለው" ማለት ነው፡፡ (ፈሊጣዊ አነጋገር የሚለውን ይመልቱ)

ደምህ በራስህ ላይ ነው

እዚህ ስፍራ "ደም" የሚያመለክተው "ደም ማፍሰስ" የሚለውን ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት/ ሲሆን የሚያያዘውም ከሞት ጋር ነው፡፡ እዚህ ስፍራ "ራስህ" የሚለው ሰውየውን እና ተጠያቂ መሆኑን የሚያመለክት ስኔክቲክ/የነገሩን ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ/ ነው፡፡ "ለሞትህ ራስህ ተጠያቂ ነህ" ወይም "ለሞትህ ምክንያት የሆንከው ራስህ ነህ" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት እና ስኔክቲክ/የነገሩን ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚሉትን ይመልከቱ)

የራስህ አፍ በራስህ ላይ መስክሯል

እዚህ ስፍራ "የራስህ አፍ" የሚለው የሚያመለክተው ሰውየውን ራሱን ነው፡፡ "በራስህ ላይ መስክረሃል" በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ስኔክቲክ/የነገሩን ስያሜ ከፊሉን በመውሰድ መላውን ነገር መግለጽ የሚለውን ይመልከቱ)

2 Samuel 1:17

አጠቃላይ መረጃ፡

ዳዊት ለሳኦልና ለዮናታን የሀዘን እንጉርጉሮ ተቀኘ

የቀስት እንጉርጉሮ

ይህ የእንጉርጉሮው ርእስ ነበር

በያሻር መጽሐፍ የተጻፈ ነበር

ይህ ለአንባቢው ወደፊት ምን ተደርጎ እንደነበር እንዲያውቅ በዝማሬው ላይ ተጨማሪ የመረጃ ዳራ ሆኖ የተጻፈ ነው፡፡ (የመረጃ ዳራ የሚለውን ይመልከቱ) የያሻር መጽሐፍ "ያሻር" የሚለው ቃል ትርጉሙ "ቀጥተኛ/በተጠንቀቅ" ማለት ነው፡፡ "የውጊያ ውሎ" መጽሐፍ በሚለው ውስጥ እንደሚገኘው፡፡ (ስሞች እንዴት ይተረጎማሉ የሚለውን ይመልከቱ)

የአንተ ክብር፣እስራኤል፣ ሞቷል

"የአንተ ክብር" የሚለው ሳኦልን ያመለክታል፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

ሃያሉ

"ሃያል" የሚለው ሀረግ ሳኦልን እና ዮናታንን ሁለቱንም ያመለክታል፡፡ ይህ ስማዊ ቅጽል የብዙ ቁጥር ነው፤ "ሃያላኑ" ተብሎ ሊገለጽም ይችላል፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት እና ስማዊ ቅጽል የሚሉትን ይመልከቱ)

ወደቀ

"ወደቀ" የሚለው ቃል በዚህ ስፍራ "ሞተ" ማለት ነው፡፡ (ዩፊሚዝም/ የማያስደስትን ቃል ሻል ባለ ቃል መተካት የሚለውን ይመልከቱ)

ይህንን በጌት አትናገሩ… በአስቀሎና መንገዶችም አታውጁ

እነዚህ ሁለት ሀረጋት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፤ የተደገሙትም የግጥሙ እንጉርጉሮ ክፍል ሆነው ነው፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

ጌት…አስቀሎና

ጌት እና አስቀሎና ከፍልስጥኤማውያን ታላላቅ ከተሞች ሁለቱ ናቸው፡፡ ሳኦልን እና ዮናታንን የገደሉት ፍልስጥኤማውያን ናቸው፡፡

የፍልስጥኤም ሴት ልጆች ሃሴት እንዳያደርጉ… ያልተገረዙት ሴት ልጆች ክብረ በዓል እንዳያደርጉ

እነዚህ ሁለት ሀረጋት ተመሳሳይ ትርጉም አላቸው፤የተደገሙትም የግጥሙ ክፍል ሆነው ነው፡፡ (ትይዩ ንጽጽራዊ ዘይቤ የሚለውን ይመልከቱ)

ያልተገረዙት ሴት ልጆች

ይህ ሀረግ የሚያመለክተው እንደ ፍልስጥኤማውያን ያሉትን ያህዌን የማይከተሉ ህዝቦችን ነው፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት የሚለውን ይመልከቱ)

2 Samuel 1:21

የጊልቦዓ ተራሮች

ዳዊት የእርሱን እንጉርጉሮ እንደሚሰሙት አድርጎ በቀጥታ ለ"ጊልቦዓ ተራሮች" ይናገራል፡፡ (አፖስተሮፊ የሚለውን ይመልከቱ)

ጠልም ሆነ ዝናብ አይገኝባችሁ

ዳዊት ንጉሥ ሳኦል በጦርነት የሞተበትን ምድር ይረግማል፣ ይህ የሚያደርገው እግዚአብሔር ለቀባው ነጉሥ ካለው ታላቅ አክብሮት/ውዳሴ የተነሳ ነው

የሃያላኑ ጋሻ ረከሰ

እዚህ ስፍራ "ሃያል" የሚለው የሚያመለክተው ሳኦልን ነው፡፡ ጋሻው የረከሰበት ምክንያት ምድር ላይ በመውደቁ እና የንጉሡ ደም በላዩ ስለፈሰሰበት ነበር፡፡ (ሜቶኖሚ/ከአንድ ባህሪው በመነሳት ለነገሩ ስያሜ መስጠት የሚለ